Saturday, 21 September 2013 11:14

…Early loss… የጽንስ መቋረጥ ...

.የሰው ልጅ እራሱን በእራሱ ተካ የሚባለው ልጅ ወልዶ መሳም ሲችል ነው ይባላል፡፡ ይህ ደግሞ እንደ አንድ የተፈጥሮ ሕግ የሚወሰድ መሆኑን ብዙዎች ያምናሉ። ነገር ግን እርግዝናው ከተፈጠረ በሁዋላ ባልታሰበ ጊዜ አደጋ ሊፈጠር የሚችልበት አጋጣሚ የተለያየ እንደመሆኑ በተቻለ መጠን ሁኔታውን በአትኩሮት መከታተል ይገባል ይላሉ ባለሙያዎቹ፡፡ በዚህ እትም ከአሁን ቀደም የእርግዝና መቋረጥን በደፈናው እስከመወለጃው ጊዜ ድረስ የተመ ለከትን ሲሆን የዛሬው ደግሞ የሚመለከተው በተለይም ቀደም ባሉት ወራት የሚከሰተውን ነው፡፡ ማብራሪያውን የሰጡን ዶ/ር ብርሀኑ ሰንደቅ ናቸው፡፡ ዶ/ር ብርሀኑ ሰንደቅ የጽንስና ማህ ጸን ሕክምና እስፔሻሊስት እና በማሪ ስቶፕስ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ የክሊኒካል አገልግሎትና የጥራት ዳይሬክተር ናቸው፡፡

                                                ----------////---------

ጥ/ Early loss… ማለት ምን ማለት ነው? መ/ እርግዝና በሶስት ወቅት የተከፈለ ነው፡፡ እሱም የመጀመሪያው ሶስት ወር ፣ቀጥሎ ያለው ሶስት ወር እና በስተመጨረሻው ያለው ሶስት ወር ነው፡፡ ርእሱ የሚያመለክተው ሁለተኛው ሶስት ወር ከማለቁ በፊት ያለውን ጊዜ ማለትም የአለም ጤና ድርጅት እንደ ሚለው ከ20-22/ሳምንት ወይንም ጽንሱ ከ500/ ግራም በታች የሚመዝን ከሆነ...ሲሆን እንደኢትዮያ ከሆነ ደግሞ ከ28/ሳምንት በታች ወይንም ከአንድ ኪሎ ግራም በታች የሆነ ውን ጽንስ ነው፡፡ ነገር ግን ትክክለኛው ትርጉም የሚሆነው ከአምስት ወር በታች ወይ ንም ከ500/ግራም በታች የሚለው ይሆናል፡፡ ጽንሱ በዚህ ጊዜ የሚቋረጥ ከሆነ በእንግ ሊዝኛው Early loss ¾ሚባል ሲሆን ይኼውም ጽንስ ከተፈጠረ በሁዋላ እድገቱን መቀ ጠል ሳይ ችል ሲቀር ወይንም በውጫዊው አለም መኖር ከማይችልበት ደረጃ ደርሶ ተቋ ረጠ ማለት ነው፡፡ በአለም የጤና ድርጅት አተረጉዋጎም መሰረት ከ20-22/ ሳምንት የሚ ለው በዚህ እድሜ ያለው ጽንስ ምናልባት ሕይወት እያለው ከማህጸን ቢወጣ እንኩ ዋን እንዲዳብርና ሳንባው እንዲሰራ የሚደረግበት ምቹ ሁኔታ እና የተሟላ የህክምና ተቋም ካለ ጽንሱ እድገቱን ሊቀጥል ይችላል ከሚል ግምት የተወሰደ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ግን ከሀያ ስምንት ሳምንት እና ከአንድ ኪሎ ግራም በታች የሆነውን ጽንስ ሕይወቱ እንዲ ቀጥል ለማድረግ የሚያስችል የህክምና ተቋም አደረጃጀት ስለሌለ በዚህ ደረጃ ያሉ ጽን ሶች እንደጠፉ ወይንም እንደተቋረጡ ይቆጠራል ማለት ነው፡፡ አገልግሎቱ በኢትዮያ አለመኖሩን በሚመለከት ምንም እንኩዋን የህክምና ባለሙያዎች ቢኖሩ እና የህክምና ተቋማቱ ቢመሰረቱም አሰ ራራቸውን እንዲሟላ በማድረግ ረገድ የህክምና መሳሪያ በማ ሟላት ረገድ የሚቀር ነገር ስላለ ለጊዜው እንደየአለም ጤና ድርጅት የጊዜ መግለጫ ሳይሆን በአገሪቱ አሰራር አስፈላጊው ይፈጸማል፡፡ ጥ/ በመቋረጥ ላይ ያለውን ጽንስ ማዳን ይቻላልን? መ/ በእርግጥ በመቋረጥ ላይ ያለ ጽንስ ሲባል የሚከፋፈሉበት ደረጃ አለ፡፡ ያለምንም እገዛ በራሳቸው የሚቀጥሉ አሉ፡፡ በድንገተኛ የህክምና እገዛ ተደርጎላቸው የሚቀጥሉ ይኖራሉ፡፡ በምን ሁኔታ ሕይወታቸው ሊቀጥል ይችላል የሚለውን ለመለየት አስቀድሞውኑ ችግሩ የተከሰተው በምን ምክንያት እንደሆነ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ጥ/ ጽንሱ የሚቋረጥበት ምክንያት ምንድነው? መ/ እርግዝና በሶስት እኩል ወራት እየተከፈለ ጊዜው የሚቆጠር ሲሆን እስከ 14 ሳምንት ከ14-28 ሳምንት ከ28- 42 ሳምንት በሚል ተከፍሎ ይታያል፡፡ በዚህም ስሌት መሰረት ከ14/ ሳምንት በፊት በራሳቸው ጊዜ የሚቋረጡ ጽንሶች በዛ ያሉ ናቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ ከ15-20 % የሚሆኑ እናቶች እርጉዝ መሆናቸውን ካወቁ በሁዋላ ጽንሱ ሊቋረጥ ይችላል፡፡ ጽንስ ለምን ይቋረጣል የሚል ጥያቄ ሲነሳ፡- 1/ አብዛኛው ምክንያት የክሮሞዞም ችግር ነው። አንድ ጤነኛ የሆነ ሰው የክሮሞዞም ሂደቱ 46XY ነው፡፡ ስለዚህ ከወንድ እስፐርም 23/ ከሴት ደግሞ 23/ ሲቀላቀል ወንድ ከሆነ XY ሴት ከሆነች XX ይሆናል፡፡ ነገር ግን በክሮሞዞም ሂደቱ የወንድና የሴት አኩል ተቀላቅሎ መሄድ ሲገባው አንዳንድ ጊዜ የወንዱ ብቻውን 46/ሆኖ ጽንሱ ሊፈጠር ይችላል፡፡ በዚህ እና ሌሎችም ተፈጥሮአዊ ችግሮች የተነሳ የክሮሞዞም ችግር ከተከሰተ ጽንሱ ወጥቶም መኖር ስለማይችል በመጀ መሪያው ሶስት ወር ጊዜ ውስጥ ይቋረጣል፡፡ ይህም 50% ድርሻ ይይዛል፡፡ 2/ ጽንሱ በራሱ በተፈጥሮአዊ አካሉ ላይ ያልተስተካከለ ነገር ሲኖር የሆርሞናል ሲስተሙ ችግር ሊኖርበት ስለሚችል ሊቋረጥ ይችላል፡፡ 3/ ከሴቶች ማህጸን ጋር በተያያዘ ለምሳሌ የአፈጣጠር ችግር ወይንም እጢ የሚኖር ከሆነ ወይንም ማህጸን ሲፈጠር ሁለት ክፍል ያለውና በሂደት ወደአንድ የሚጠቃለል ሲሆን ይህ አካሄዱ የተዛባ ከሆነ ጽንሱን እንዳያድግ ምክንያት ይሆነዋል፡፡ 4/ በስኩዋር ሕመም ወይንም በታይሮይድ እጢ ምክንያት ጽንስ ሊቋረጥ ይችላል፡፡ 5/ እንግዴ ልጁ አካባቢ ኢንፌክሽን ሲኖር...ወዘተ በመሳሰሉት ችግሮች ጽንስ ሊቁዋረጥ ይችላል፡፡

ጥ/ አብዛኛውን ጊዜ የጽንስ መቋረጥ ሚገጥማቸው ሴቶች ምን አይነት ናቸው? መ/ ዋናው እድሜ ነው፡፡ እድሜ እየገፋ በመጣ ቁጥር ካለምንም ምክንያት ጽንስ ሊቋረጥ ይችላል። እድሜዋ ከ40/አመት በላይ የሆነች ሴት ጽንሱ ሳይቋረጥ የመውለድ እድሉዋ 30 % ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ እድሜ በራሱ ካለምንም ሌላ ተጨማሪ ምክንያት ጽንስ እንዲቋረጥ ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡ ሌላው የተለያዩ የባህርይ ችግሮች...ለምሳሌ ሲጋራ ማጨስ...አደንዛዥ እጽ መጠቀም ...አልኮል በብዛት መውሰድ በመሳሰሉት ምክንያቶች ሴቶች የጽንስ መቋረጥ ሊገጥማቸው ይችላል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ከልክ ያለፈ የአካል ውፍረትና ቅጥነት ለጽንስ መቋረጥ ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የውስጥ ሕመሞች ማለትም እንደስኩዋር እና ደምግፊት የመሳሰሉት ለችግሩ ሊዳርጉ ይችላሉ፡፡ በእርግጥ የደም ግፊት ብዙውን ጊዜ ከ20/ሳምንት በፊት ባለው የእርግዝና ወቅት ባይከሰትም ነገር ግን አስቀድሞ ሕመሙ ካለ እና ምናልባትም እርግዝናው ቀኑን እየገፋ ከመጣ እንደአንድ ችግር የሚቆጠር ነው፡፡ ጥ/ ጽንሱ በመቋረጥ ላይ መሆኑን እናትየው በምን ልታውቅ ትችላለች? መ/ ጽንሱ በመቋረጥ ላይ መሆኑን ለመገመት ሰውነትን ማዳመጥ ይጠቅማል፡፡ አንዲት ሴት በእርግዝና ላይ እያለች ደም ከፈሰሳት የደም መልኩ ንጹህ ቀይ ወይንም ቡና አይነት ሊሆን ይችላል፣ በሆድ እቃ ወይንም ፊኛ አካባቢ ሕመም ከተሰማት፣ የሚፈሰው ደም የረጋ ወይንም እንደስጋ መሰል ነገር ከሆነ እርግዝናው እየቀጠለ ነው ለማለት ያስቸግራል፡፡ በእርግጥ የሆድ ሕመም ምልክት ወይንም ደም መፍሰስ የሚባለው ሁልጊዜ የጽንስ መቋረጥ ምልክት ይሆናል ማለት አይደለም፡፡ የሌሎች ምክንያቶችም ምልክቶች ሊሆን ይችላል ፡፡ ለምሳሌ ከማህጸን ውጭ እርግዝና ሲከሰትም በቱቦ ውስጥ ስለሚቆይ በሚኖረው ምቹ ያልሆነ ስሜት የሆድ ሕመም ወይንም የደም መፍሰስ ሊያጋጥም ይችላል፡፡

ስለዚህም ወደህክምና ተቋም መሄድ አስፈላጊ ይሆናል፡፡ ጥ/ ጽንስ ከተቋረጠ በሁዋላ ለቀጣዩ ጊዜ ምን ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል? መ/ ጽንስ ሲቋረጥ የህክምና ድጋፍ ከተደረገ በሁዋላ የደም መፍሰስ ስለሚኖር የደም መፍ ሰሱ እስኪቆም ድረስ ቢያንስ እስከሁለት ሳምንት ግንኙነት ማድረግ አያስፈልግም፡፡ በመጸዳዳት ወይንም በመታጠብ ጊዜ ከኢንፌክሽን ለመጠንቀቅ ሲባል እጅን ወደውስጥ አስገብቶ መታጠብ ትክክል አይሆንም፡፡ እንደ አንዳንድ ጥናቶች ጽንስ ከተቋረጥ በሁዋላ በአስረኛው ቀን ሴቶች የዘር ፍሬ እንደላኩ የሚያሳይ ሲሆን ነገር ግን በተቻለ መጠን ቀጣዩን እርግዝና ከ3-6ወር ድረስ ማዘግየት አስፈላጊ መሆኑን ማወቅ ይገባል፡፡ ምክንያቱም አንዳንድ የህምና ድጋፍ ለማድረግ ፣የሚሰጥ መድሀኒት ካለ ለመውሰድ እንዲሁም የሰውነት መጠንከር እንዲኖር አስፈላጊውን ጊዜ ማግኘት አስፈላጊ ስለሚሆን ነው ፡፡ ጽንስ ከተቋረጠ በሁዋላ ማህበራዊና ስነልቡናዊ ችግርን ሊያስከትል ይችላል፡፡ አባትም እንደአባት የሐዘን ስሜት ሊኖረው ሲችል በተለይም እናትየው መደበት፣ መጨነቅ፣መበሳጨት ፣ማልቀስ የመሳሰለው ሁሉ ሊኖራት ይችላል፡፡ በዚህ ሰአት ከቤተሰብም ሆነ ከባለሙያ ከፍተኛ ድጋፍ ያስፈልጋቸዋል፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

በ1995 ዓ.ም ለአዲስ አበባ ዘጠነኛ ሆኖ ሊፀድቅ የተዘጋጀው የከተማ ፕላን ይፋ ከመሆኑ በፊት የከተማው ነዋሪ እንዲወያይበትና ሃሳቡን እንዲሰጥ የሚችልበት መድረክና ኤግዚቢሽን ተዘጋጅቶ ነበር፡፡ መስቀል አደባባይ በሚገኘው አዲስ አበባ ሙዚየም ለወራት በቆየው ኤግዚቢሽንና የውይይት መድረክ ላይ ትኩረት ስበው ከነበሩት ርእሰ ጉዳዮች መካከል በመሃል ፒያሳ ሊገነባ ስለታቀደው ባለ 40 ፎቅ ሕንፃ ይሰጥ የነበረው ማብራሪያ አንዱ ነበር፡፡ “አባወራ የሌለበት የሴት ቤትና ባዶ መሬት ተመልካቹ ብዙ ነው” እንደሚባለው የፒያሳው ቦታ ለ40 ፎቅ መስሪያ ከመታሰቡ በፊት የብዙ ታሪካዊ ነገሮች ሥፍራ ነበር፡፡ ከጣሊያን ወረራ በፊት ከፊል የአራዳ ገበያ መደብሮች ቦታው ላይ ነበሩ፡፡ በኋላ ላይ የሩስያ ባህል ማዕከል የመጀመሪያው ቤት፣ የእንዳልካቸው መኮንን ቤተ መፃህፍት፤ ኪንግ ጆርጅ ቡና ቤት… የመሳሰሉ ታሪካዊ ቅርሶች ነበሩበት። ቤቶቹ ከፈረሱ በኋላ በስፖርት ማዘውተሪያ ቦታነት ለብዙ ዓመታት አገልግሏል፡፡ በደርግ ዘመን የመስቀል ደመራ በዓል ሥነ ስርዓት ማከናወኛም ሆኖ ነበር፡፡

ኢሕአዴግ ስልጣን ከያዘ በኋላ ሜዳው በኳስ መጫወቻነት ለተወሰኑ አመታት አገልግሏል፡፡ በመጨረሻ ለአልሚ ባለሀብት ተሰጠ…. በውይይት መድረኩ በፒያሳው መሬት ላይ ባለ 40 ፎቅ ሕንፃ መሥራቱ በአይነቱ የመጀመሪያ ስለሚሆንና ለአዲስ አበባም የእድገት ምልክት ነው የሚል አስተያየት የሰጡ ቢኖሩም በተቃራኒው ሜዳው ላይ ያን ያህል ርዝመት ያለው ሕንፃ መሰራት የለበትም ብለው የሚቃወሙም ነበሩ። የተቃዋሚዎቹ ምክንያት ሊገነባ የታሰበው ሕንፃ በአካባቢው ያሉ ነበር ሕንፃዎችን ውበትና ታሪካዊነት ያደበዝዛል የሚል ነው፡፡ ቦታው ላይ የጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን፤ የአፄ ምኒልክ ሐውልት፤ በአቡነ ጴጥሮስ ላይ ጣሊያኖች የሞት ፍርድ የሰጡበት ቤትና የጳጳሱ ሐውልት፣ የኢየሩሳሌም መታሰቢያ ሕንፃ፤ አሮጌና አዲሱ የማዘጋጃ ቤት ሕንፃዎች፤ በአርመን፣ በግሪክ፣ በሕንድና በጣሊያኖች የተሰሩ የመኖሪያና የንግድ ቤቶች ይገኛሉ፡፡

ነባሮቹ ህንፃዎችና ሃውልቶች አንዳቸው ሌላኛቸውን ሳይጫኑ፣ ለአካባቢው ውበት ፈጥረዋል፡፡ ባለ 40 ፎቅ ሕንፃ በአቅራቢያቸው ቢገነባ ውበታቸው ድራሹ ይጠፋል፡፡ ታሪካዊነታቸው እንዲደበዝዝ ምክንያት ይሆናል በሚል ነበር የግንባታው ሃሳብ ተቃዋሚዎች አስተያየታቸውን የሰጡት፡፡ በደርግ ዘመን የተገነባው የ”አራዳ ሕንፃ” በአካባቢው ላይ የፈጠረውን ጫና እንደማሳያ ያቀረቡ ሰዎችም ነበሩ፡፡ ይህንን ታሪካዊ ክስተት እንዳስታውስ ምክንያት የሆነኝ ከሰሞኑ በአሊያንስ ኢትዮ ፍራንስ የቀረበው የፎቶግራፍ ኤግዚቢሽን ነው፡፡ “የተዘነጋ ቅርስ” በሚል ርእስ የአፍሪካ መዲና (አዲስ አበባ) የመጀመሪያዎቹ 50 አመታት ኪነ ሕንፃ ፎቶ አውደ ርዕይ አዘጋጅተው ያቀረቡት አርክቴክት ፋሲል ጊዮርጊስና ህላዊ ዮሴፍ ናቸው፡፡ ጳጉሜ 4 ቀን የተከፈተው አውደ ርዕይ እስከ መስከረም 16 ቀን 2006 ዓ.ም ድረስ ለሕዝብ ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡ በተለያዩ ተቋማት ባለሙያዎችና ግለሰቦች ትብብር ለእይታ የበቃው ኤግዚቢሽን፤ ታሪካዊና መረጃ ሰጪ ፎቶግራፎችን አቅርቧል - ከግርጌ ማስታወሻ ጋር፡፡ ወደ ኤግዚቢሽኑ አዳራሽ መግቢያ በር ላይ የተመልካቹን ቀልብ የሚስብ ፎቶግራፍ ይታያል፡፡

የአውደ ርእዩ አካል ያልሆነው ይህ ምስልና መግለጫው ስለ 1911 ዓ.ም ነው መረጃ የሚሰጡት፡፡ በዚያን ዘመን ፈረንሳዊያን በዚያው ግቢ ውስጥ ኢትዮጵያውያን ሕፃናትን ሰብስበው ሲያስተምሩ ያሳያል፡፡ በአውደ ርእዩ ስብስቦችም የዚህኑ ታሪክ እውነታ የሚያረጋግጥ ተጨማሪ ፎቶግራፍ ቀርቧል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ እ.ኤ.አ ከ1886 እስከ 1936 ባሉት 50 አመታት ከተገነቡ ቤቶች 36 ያህሉ የት እንደሚገኙ፣ መቼ እንደተሰሩ፣ በማንና በምን ማቴሪያል እንደተገነቡ፣ እንዴት ሊሰሩ እንደቻሉ ጭምር በፅሁፍና በፎቶግራፍ የሚያስቃኘው አውደ ርእይ ካቀረባቸው መሐል በቤተ መንግሥትና በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ግቢ የሚገኙ አዳራሾች፤ የጣይቱ ሆቴልና የንግሥት ዘውዲቱ እንግዳ ማረፊያ አይነት ልዩ ስራዎች፤ የሙሴ ሚናስና የአልፍሬድ ኢግል አይነት ኢንጂነሮች መኖሪያ፤ የነጋዴና ባለስልጣን ቤቶች፤ የእንግሊዞች መፅሐፍ ቅዱስ ማህበር መገኛ የነበረ ሕንፃ፤ እንደ ሰይጣን ቤት ልዩ ስያሜ የተሰጣቸው ግንባታዎች… ከፊሎቹ ናቸው፡፡ አንድ ሕንፃ ወይም መንደርን በ50 አመታት ልዩነት በተነሱ ሁለት ፎቶግራፎች አማካኝነት ከሚያሳዩ ፎቶግራፎች አንዱ የማህተመ ጋንዲ ጐዳና ነው፡፡ ጐዳናውና የመንደሩ ቤቶች እ.ኤ.አ በ1960 እና በ2013 በተነሱት ፎቶዎች፤ የተጠበቀውና የጠፋውን ያመለክታሉ፡፡ አካባቢው እንዲህ ቢሆንስ በሚል በቀረበው ፕሮፖዛል ማሳያ ምስል ደግሞ የጠፋውና የተበላሸው ታድሶ፣ የጐደለው ሞልቶ ይታያል፡፡

የሙሴ ሚናስ መኖሪያ ቤትም በተመሳሳይ መልኩ በ50 አመታት ውስጥ የሚታይበትን ለውጥ የሚያስቃኙ ፎቶግራፎች ቀርበውለታል፡፡ ከእሪ በከንቱ ወንዝ በላይ ወደ ፒያሳ በሚያደርሰው ጐዳና የሚገኘው የዚህ ቤት ባለቤት አርመናዊ መሆናቸውን፣ በሙያቸውም መሐንዲስ እንደነበሩ እና መኖሪያ ቤታቸውም ለአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያው ባለ 4 ፎቅ ሕንፃ እንደሆነ ከአውደ ርእዩ መረጃው መረዳት ይቻላል፡፡ በዚህ ታሪካዊ ቤት 25 አባወራ ቤተሰቦች እየኖሩበት እንደሆነም መረጃው ሲያመለክት፤ እንዲህ ቢሆንስ በሚል የቀረበው ፕሮፖዛል አመልካች ምስልም የታሰበለትን ሆኖ ባየነው የሚያስብል ነው፡፡ ሰኞ መስከረም 6 ቀን 2006 ዓ.ም ምሽት በአውደ ርዕዩ ላይ የውይይት መድረክም ተዘጋጅቶ ነበር፡፡ በአሊያንስ ኢትዮ ፍራንሴስ ግቢ በተሰናዳው መድረክ ላይ የጥናት ፅሁፍ ያቀረቡት አርክቴክት ፋሲል ጊዮርጊስ “በአዲስ አበባ ከተማ ከልማት ሥራ ጋር በተያያዘ ከፍተኛ የሆነ ለውጥ ያለ መሆኑ የሚታይ ቢሆንም ለሥራው እውቅና የሰጠን አይመስልም” በሚል የመግቢያ ንግግር ጀምረው ስለ “የተዘነጋው ቅርስ” ሰፋ ያለ ማብራሪያ አቅርበዋል፡፡

አዲስ አበባ በነዋሪዎቿ ፈቃድና ተነሳሽነት ያለ ምንም የከተማ ፕላንና መመሪያ መገንባት መጀመሯን ያመለከቱት አርክቴክቱ፤ ይህ ደግሞ እስካሁንም አልቀረፍ ላለው ችግር መሰረት መሆኑን ገለፁ፡፡ የአድዋ ጦርነት ድል ኢትዮጵያ አለም አቀፍ ትኩረት እንድታገኝ ምክንያት በመሆኑ፤ አዲስ አበባ የበርካታ አገራት ዲፕሎማቶች መገኛ እንድትሆን አስተዋፅኦ ማድረጉንና የከተማዋ ታሪካዊ የግንባታ ሥራዎች የውጭዎቹ አሻራ እንዲያርፍበት አድርጓልም ብለዋል፡፡የ1928ቱ የጣሊያን ወረራ በኢትዮጵያ ላይ ካስከተለው ጉዳት ባሻገር፣ በአዲስ አበባ ከተማ ላይ ካስገኘው ጥቅሞች መካከል ፕላንን መሰረት ያደረጉ የግንባታ ሥራዎች መሰራታቸውና መታቀዳቸው ተጠቃሽ እንደሆነም ተነግሯል፡፡ ከዚያ በኋላ የከተማ መሪ እቅድን የተከተሉና ያልተከተሉ የግንባታ ሥራዎች መሰራታቸውን፤ አዲስ አበባም ከእለት ወደ ዕለት እየሰፋችና እያደገች መምጣቷን አብራርተው፤ የታሪካዊ ቤቶች ጉዳይ አደጋ ላይ ስለመሆኑን በተለያዩ ማሳያዎች አስደግፈው ገልፀዋል፡፡ የመንግሥትና የሕብረተሰቡ የለውጥ ፍላጐት ለቅርሶች ትኩረት እንዳይሰጥ አንዱ ምክንያት እንደሆነም ተነግሯል፡፡ በፊት በጉለሌና ቦሌን በመሳሰሉት የከተማዋ ዳርቻዎች በቀላሉ ይገኝ የነበረው መሬት አሁን የቦታ ፈላጊዎች ቁጥር መበራከት ቅርሶችን ለአደጋ ያጋለጠ የመሬት ሽሚያ መፍጠሩም ሌላው ምክንያት ነው ተብሏል፡፡

አዲስ አበባ ከተማ ታሪካዊ ቤቶችን መጠበቅ አለመቻል ብቻ ሳይሆን ለተለያዩ ግልጋሎት ሊውሉ የሚችሉ ክፍት ቦታዎችም እያጣች መምጣቷ ከዚሁ ጋር በተገናኘ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በመንግሥትም በሕብረተሰቡም ዘንድ ታሪካዊ ቤቶችን መጠበቅ ስለሚያስገኘው ጠቀሜታ ግንዛቤው ያለ አይመስልም ያሉት አርክቴክት ፋሲል ጊዮርጊስ፤ ለውጡ ሊመጣ የሚችለውና ችግሩም የሚቀረፈው፤ ሕብረተሰቡን ግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት በተከታታይ በመስጠትና ለቅርሶችም ሕጋዊ ከለላና ጥበቃ በማዘጋጀት ነው ብለዋል፡፡ በተለይ በህብረተሰቡ ዘንድ ያለው ግንዛቤ በጣም አነስተኛ ነው ያሉት ጥናታዊ ፅሁፍ አቅራቢው፤ የሚኖሩባቸውን ታሪካዊ ቤቶች የአጥር እንጨት እየመዘዙ ለማገዶ የሚጠቀሙ አሉ፤ ታሪካዊ ቤቶቹ ይታደስ ሲባል ሞቼ እገኛለሁ፤ ሙዚየም ሊሆን ነው ልቀቁ ሲባሉ አሻፈረኝ የሚሉ… ነዋሪዎች ጥቂት እንዳልሆኑ ገልፀዋል፡፡ከቅርስና ታሪካዊ ስራዎች ጋር በተያያዘ የሐረር፣ የአክሱም፣ የጐንደር… ምሳሌዎችን እያቀረቡ ማብራራታቸውን የቀጠሉት አርክቴክቱ፤ ለቱሪስቶች ደረጃውን የጠበቀ ሆቴልና ማረፊያ ለመሥራት እየጓጓን ቱሪስቶችን ለሚስበው ታሪካዊ ቅርስ ትኩረት አለመስጠት ያነጋግራል በማለት ገለፃቸውን ቋጭተዋል፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 21 September 2013 11:09

ያላለቀ ድርሰት

     “ኧረ ይብቃህ ደጀኔ!... አራት ሰዓት ሞላኮ!...” አሉ እትየ ስንዱ፣ መጋረጃውን ገለጥ አድርገው ከወደ ጓዳ ብቅ እያሉ፡፡ “አንቺ ግን ለምን ሰላም አትሰጪኝም!?...” ደጀኔ አቀርቅሮ ከሚጽፍበት ቀና በማለት በንዴት ጦፎ እስክርቢቶውን ወረወረ፡፡ “ስንቴ ልንገርሽ አክስቴ!?… በውስጤ የታመቀውን የደራሲነት ስሜት መተንፈስ እንጂ፣ የኮሌጅ ትምህርት አጠናቆ መመረቅ አይደለም የህይወቴ ጥሪ!” እየተንቀጠቀጠ ተናገረ፡፡ “የዛሬውስ የተለየ ነው!... ገና በማለዳ ንትርክ ጀመራችሁ?” የእማማ በለጡ ድምጽ በስተቀኝ ያለውን የኮምፔርሳቶ ግድግዳ አልፎ ተሰማ፡፡ ከጉዳይ የጣፋቸው አልነበረም፡፡ “ተው እንጂ ደጀኔ… ደህና ሂደህ ሂደህ አንድ አመት ሲቀርህ አትሰላች!” በትህትና መለሱለት፡፡ “አንቺኮ ችግርሽ ይሄ ነው!... የጀመርኩትን ትምህርት እንጂ፣ የጀመርኩትን ድርሰት ስለመጨረሴ አትጨነቂም!” ከተቀመጠበት ብድግ አለ፡፡ ሁለት አንቀጽ ጅምር አጭር ልቦለድ የጻፈባትን ወረቀት ከጠረጴዛው አንስቶ በፍጥነት ወደ ጓዳ አመራ፡፡

“እኔኮ ላንተ ብየ ነው!... ደሞም’ኮ አትጣፍ አላልኩህም፡፡ ከኮሌጅ ስትመለስ መጨረስ ትችላለህ” አሉት አክስቱ በትህትና ፈገግ ብለው፡፡ የአክስቱ ትህትና የገነፈለ ስሜቱን በረድ አደረገለት፡፡ እንደወትሮው አልተቆጡትም፡፡ እንደሌላው ጊዜ ልብ የሚሰብር ነገር አልተናገሩትም፡፡ “ደሞ አንተን ብሎ ደራሲ!... የአስር ሳንቲም ሻይ ቅጠል የማይገዛ እንቶፈንቶ መሞንጨሩን ትተህ፣ ትምህርትህን ብታጠና ይሻልሃል!” ብለው አልተሳለቁበትም፡፡ ወደ ጓዳ የጀመረውን ጉዞ ገታ አደረገና ዘወር ብሎ ተመለከታቸው፡፡ አክስቱ ፊት ላይ ባዕድ ፈገግታ ተመለከተ፡፡ ጥቂት አሰብ አደረገና በእጁ የያዘውን ወረቀት በተስፋ መቁረጥ ወደ ጓዳ ወረወረው፡፡ “ማንም ተጠያቂ አይደለም…” ብሎ ጀምሮ፣ ሁለት አንቀጽ ከተጓዘ በኋላ ሳይቋጭ የቀረው የደጀኔ ጅምር አጭር ልቦለድ፣ እየተውለበለበ ወርዶ ጓዳ የተቀመጠ መክተፊያ ላይ አረፈ፡፡ ደጀኔ ከአክስቱ ቤት ወጥቶ ወደ ኮሌጅ ሄደ፡፡

ደጀኔ ከኮሌጅ ወጥቶ ወደ አክስቱ ቤት ተመለሰ፡፡ ከላይ ባሉት ሁለት አረፍተነገሮች መካከል ብዙ ነገር ተከናውኗል፡፡ “ስንዴ ቡናው ፈልቷል” ብለዋል እማማ በለጡ፡፡ ደጋግመው ተጣርተዋል… ምላሽ አጥተዋል፡፡ ወደ እትየ ስንዱ ቤት መጥተዋል፡፡ “የት ገባች ይቺ ሴትዮ?” ጠይቀዋል - ስንዱን ከሳሎን ሲያጡ፣ ወደ ጓዳ እያዩ መጋረጃውን እየገለጡ፡፡ “እሪሪሪሪሪ!!!!!” ብለዋል በፍርሃትና በድንጋጤ እየተንቀጠቀጡ፣ መንደሩን በጩኸት እያቀለጡ፡፡ እትዬ ስንዱ ተፈጽመዋል፡፡ በእንስራ ገመድ ራሳቸውን አንጠልጥለዋል፡፡ መንደርተኛው በለቅሶ ሲናወጥ፣ ዙሪያ ገባው በዋይታ ሲቀወጥ፣ ልጅ አዋቂው በእንባ ሲራጭ… ይህ ሁሉ ሲሆን ከቆየ በኋላ ነው፣ ደጀኔ ከኮሌጅ ወደ መንደሩ የተመለሰው፡፡ ያዙኝ ልቀቁኝ አለ - ደጀኔ የሆነውን ሁሉ ሲሰማ፡፡ “አክስቴን… ስንዱዪን!... ምነው ምን አረግኩሽ!?... ለማን ትተሽኝ ሄድሽ?... እኔ ልሰቀልልሽ!...” እያለ መሬት ላይ ወድቆ ተንከባለለ፡፡ ጎረቤት ተባብሮ ከመሬት ሲያነሳው ደግሞ፣ ለመሮጥ ሞከረ፡፡ ወዴት?... ወደ እማማ በለጡ ውሃ ጉድጓድ!... ለምን?... ራሱን ለማጥፋት! “የኔ ጉድጓድ የማንም እርኩስ መደበቂያ ነው እንዴ?!” አሉ እማማ በለጡ ነገሩን ሲሰሙ፡፡ ደጀኔ ሴትዮዋ “መደበቂያ” የሚለውን ቃል ያለነገር እንዳልተጠቀሙት የገባው ዘግይቶ ነው። ጎረቤቶቹ አረጋግተው ካስቀመጡትና የሆነውን ሁሉ ከነገሩት በኋላ ነው ነገሩ የተገለጠለት፡፡

ፖሊስ ነገሩን ሊያጣራ መጥቶ እንደነበርና መረጃ ሰብስቦ እንደሄደ ከጎረቤት ሰማ፡፡ እማማ በለጡ ፖሊሶች ከሄዱ በኋላ የእሱን ስም እየጠሩ አጉል ነገር ሲናገሩ እንደነበር ተነገረው፡፡ “ጧት ስንዱና ደጀኔ ሲጨቃጨቁ ሰምቻለሁ፡፡ እሱ ከሄደ ከጥቂት ጊዜ በኋላ፣ ቡና ጠጪ ልላት ስሄድ ተንጠልጥላ አገኘኋት፡፡ እሱ ነው አበሳጭቶ ያለጊዜዋ የደፋት” ሲሉ ነበር አሉት፡፡ ስለዚህ ደጀኔ በአክስቱ ሞት ተጠርጣሪ ነው። ለምርመራ ወደ ምኒልክ ሆስፒታል ከተወሰደው አስከሬን ጋር የሄደች አንዲት ሴት “ፖሊሶቹ ስንዱ ከመሞቷ በፊት የጻፈችውን ኑዛዜ አግኝተዋል” የሚል አዲስ መረጃ ይዛ መጣች፡፡ ይህ ነገር ብዙዎችን አስደነቀ፡፡ ‘እሱ ነው አቃጥሎ የገደላት’ ብለው፣ ደጀኔን ውስጥ ውስጡን ሲያሙ የነበሩ ሁሉ ተገረሙ፡፡ ደጀኔም ቢሆን ወሬውን ሲሰማ ግራ መጋባቱ አልቀረም። አክስቱ መጻፍ እንደሚችሉ አያውቅም ነበር። ይሄም ሆኖ ከተጠያቂነት ነጻ የሚያደርገው የአክስቱ ኑዛዜ በመገኘቱ ተጽናና፡፡

በዚህ መሃል ነው መርማሪው ፖሊስ ከተፍ ያለውና ከደጀኔና ከቅርብ ሰዎች ጋር መወያየት የጀመረው፡፡ ተገኘ የተባለው ጽሁፍ በሌላ ሰው ሆን ተብሎ የተቀነባበረ ሴራ አለመሆኑንና እርግጥ ሟቿ የጻፉት እንደሆነ ለማረጋገጥ፣ ሌላ ከዚህ በፊት የጻፉት ጽሁፍ ካለ እንዲቀርብለት አዘዘ ፖሊሱ፡፡ ያልተበረበረ ቁምሳጥንና ሻንጣ የለም፡፡ ደጀኔ ወደ ጓዳ ገብቶ የአክስቱን የእጅ ጽሁፍ መፈለግ ጀመረ፡፡ የአክስቱ የእጅ ጽሁፍ ጓዳ የለም። የአክስቱ ብቻ ሳይሆን የእሱም የእጅ ጽሁፍ የለም፡፡ “ማንም ተጠያቂ አይደለም…” ብሎ ጀምሮ፣ ሁለት አንቀጽ ከተጓዘ በኋላ ሳይቋጭ የቀረው ጅምር አጭር ልቦለዱ፣ ጧት ላይ ተናዶ ወደ ጓዳ የወረወረው የእጅ ጽሁፉ! ደጀኔ ነገሩ ተገለጠለት፡፡ የለቀስተኛ ድምጽ እየረበሸው፣ ጓዳ ተደብቆ የሆነ ነገር ለመጻፍ ሞከረ… የሆነ ነገር… በቃ… አለ አይደል… ለፖሊሶቹ የሚሆን… ከጓዳ ያገኙትን የአክስቱን ኑዛዜ ትክክለኛነት ለማረጋገጥ የሚረዳ የአክስቱ የእጅ ጽሁፍ…

Published in ልብ-ወለድ
Saturday, 21 September 2013 10:59

የጀግና አሟሟት

ምዕራፍ አንድ፡- አጼ ቴዎድሮስ እና ሞት

አትጠገብ የምትባል ሴት ከ195 አመታት በፊት ወንድ ልጅ ወለደች፡፡ ወይዘሮ አትጠገብ ሀይለ ጊዮርጊስ ከሚባል ውድ ባለቤቷ ካሣ የሚባል ልጅ ወለደች፡፡ ልጁ ካሣ ሀይሉ ተብሎ ይጠራ ነበር፡፡ ካሣ ሲያድግ ንጉስ መሆን አማረው፡፡ ካሣ በተወለደበት ዘመን ተራ ሠው አይነግስም፡፡ ነገሥታት የሚሆኑት የሠለሞን ዝርያ ያላቸው፣ በእግዚአብሔር የተመረጡ እና የተሰየሙ እናም የነዚህ ሠዎች ዝርያዎች ነበሩ፡፡ ካሣ ግን ንጉሥ መሆን አማረው፡፡ ሲያስብ እንዲህ እያለ ነበር ፡- “የነገስታቱ ዝርያ አይደለሁም፡፡” “እና ባልሆንስ?!” “አትቆጣ?!” “መቆጣት አይደለም፡፡” “እና ታዲያ;!” “ንጉሥ መሆን አምሮኛል!” “እና ንጉሥ መሆን የምችል ይመስልሃል?!” “Yes, I can” ብሎ ተነሳ፡፡ የአሜሪካው ንጉስ ባራክ ኦባማ `Yes, we can` የሚለውን የምርጫ መወዳደሪያ መፈክር የኮረጀው ከካሳ ሀይሉ ነው፡፡ የምናውቅ እናውቃለን፡፡

ካሳ ጉረኛ አልነበረም፤ በተወለደ በሰላሳ ሰባት አመቱ፣ ዳግማዊ ቴዎድሮስ ተብሎ በደረስጌ ማርያም ቤተ-ክርስቲያን ንጉሰ ሆኖ ተቀባ፡፡ ካሳ ተራ ንጉስ አልነበረም፤ ሀገሩን በጣጥሰው ሲገዙ የነበሩትን ቅርብ ሀሳቢ መሳፍንት አስገብሮ ንጉስ ነገስታቸው ሆነ፡፡ ያልተረጋጋች እና ያልሰለጠነች ኢትዮጵያን ለማረጋጋት እና ለማሰልጠን ጣረ፤ ለአስራ ሶስት አመታት ነገሰ፤ ባከነ፡፡ ከንግስናው እለታት አንድ ቀን መሞቻህ ይሁን ሲለው፣ እኩያው አድርጎ ለሚያስባት የእንግሊዝ ንግስት የቴክኒክ ድጋፍ የሚጠይቅ ደብዳቤ ፃፈ፤ ፅፎም ካሚሮን ለሚባል እንግሊዛዊ፣ እንዲያደርስ ላከው፡፡ መልእክተኛው ግን የቁራ መልእክተኛ ሆነ። ካሜሮን የተላከውን መልእክት ሳያደርስ፣ በዚያም ላይ ግብፅ ምናምን ሲዞር ከርሞ መጣ፤ በወቅቱ የግብፅ ሰዎች ከቴዲ ጋር አሪፍ ጓደኞች አልነበሩም፡፡ ካሜሮን መጣ፡፡

“እህሳ ነጫጭባው! መልእክቴን ለንደን አደረስሽ?” “አላደረስኩም ነብሴ፤ ግን እንዲደርስ በሌሎች ልኬያለሁ፡፡” “እኔ እኮ መልእክቱን አንቺ እራስሽ ለንደን ወስደሽ ለንግስቲቷ በእጇ እንድታስረክቢ ነው የላኩሽ፡፡” “ፍሬንድ እኔ እሱ መች ጠፋኝ፤ አለቆቼ እኛ በምናደርሰው መንገድ እናደርሰዋለን አሉኝ እንጂ፡፡” “እና ይህን ሁሉ ጊዜ ምን ስታደርጊ ከርመሽ መጣሽ?!” “ግብፅ ምናምን ለአንዳንድ ጉዳዮች ሄጄ ነበር፡፡” “እንዲህ ነኝና መይሳው!” አለ ንጉስ ቴዎድሮስ፤ በጣም ተናዷል ፡፡ “ይህችን ነጫጭባ አስገባት፡፡” ካሜሮን እስር ቤት ገባ፤ ታሰረ፡፡ የካሜሮን አቢሲኒያ ውስጥ መታሰር ለንደን ተሰማ፡፡ እንግሊዝ ካሜሮንን ለማስፈታት ራሳም የሚባል ሰውዬ ላከች፤ ቴዲ እሱንም ጭፍራዎቹንም አሰራቸው፡፡

ቴዲ ሳይታወቀው አንገቱ ላይ ገመዷን እያጠበቀ ነበር፡፡ ቴዎድሮስ የታሪካችን ፈርጥ፣ የስነ-ፅሑፋችን ጌጥ ነው፡፡ እስከአሁን ካነበብኳቸው የአማርኛ መፅሐፍት የብርሃኑ ዘርይሁንን “የታንጉት ምስጢር” የሚያክል የለም፡፡ ቴአትር ብዙ አላየሁም፣ ካየኋቸው ግን የፀጋዬ ገብረ መድህንን “ቴዎድሮስ” የሚስተካከል የለም፡፡ ምዕራፍ ሁለት፡- እኔና ሞት የአንድ ሠው የህይወት ዘመን ሶስት ክፍሎች ናቸው ያሉት፡፡ አንድ፡- ጅማሮ፤ ሁለት፡- ኑሮ፤ ሶስት፡- ሞት፡፡ ሶስቱም እኩል ዋጋ አላቸው፡፡ ቴዎድሮስ ከህይወቱ አጀማመር እና አኗኗር በጣም ጎልቶ የሚነገረው አሟሟቱ ነው፡፡ የጀግና አሟሟት ተምሳሌት ተደርጎ ሁሌ ነው የሚወራው፡፡…. እኔ ደግሞ ብዙ ጊዜ ያልተሳኩ እራስን የማጥፋት ሙከራዎች አድርጌያለሁ፤ እንደ ሲልቪያ ፕላዛ። ሲልቪያ ፕላዛ ሶስት የከሸፉ እራስን የማጥፋት ሙከራዎች አድርጋ፣ በሶስት መክሸፍ አንድ የተሳካ ግጥም ፅፋለች፡፡ የከሸፉ እራስን የማጥፋት ሙከራዎች ትዝ ባሉኝ ጊዜ (ሁሌ ነው ደግሞ ትዝ የሚሉኝ) ቴዎድሮስ ትዝ ይለኛል፡፡ እራስህን ማጥፋት የምር እየፈለክም ላይሳካልህ ይችላል፡፡ ቴዎድሮስ ደፋር ብቻ ሳይሆን እድለኛም ነበር። ሁሌ ስለ ቴዎድሮስ አስባለሁ፤ ሁሌ ትዝ የሚልህ ምርጥ መጽሐፍ “የታንጉት ምስጢር” ከሆነ፤ ያው ቴዎድሮስ ነው ትዝ የሚልህ፡፡ አንድ ቀን ስለህይወት ከንቱነት እያሰብኩ፤ (ቀጣዩን ራሴን የማጥፋት ሙከራዬ የመግቢያ ሀሳብ ነው፤ ከልምድ አውቃለሁ) የሚገርም ነገር ተከሰተ፡፡ የቴዎድሮስ አይነት የክብር አሟሟት ተከስቶ አየሁ። የሚገርመው ደግሞ ብዙ ሠው ተሰብስቦ በነበረው ባር ድርጊቱን ከመጀመሪያው እስከመጨረሻ ስከታተል የነበርኩት እኔ ነኝ፡፡ ለኔ የተላከልኝ መለኮታዊ መልእክት ይመስለኛል፡፡ ቴሌ ባር የሚባል ቤት ውስጥ የመቅደላ ታሪክ ሲደገም፤ ሙሉ(!) ታሪኩን ያየሁት እኔ ብቻ ነበርኩ። ታሪክ መፃፍ አለበት፤ በተለይ እንዲህ አይነቱ፡፡ የክስተቱ ሙሉ ተመልካች (ነበርኩ) ነኝ ብያለሁ። አሁን የምፅፍላችሁ ግን ድርጊቱ ከተከሰተ በኋላ ስለ ሠዎቹ ያጠናከርኩትን አካትቼ ነው፡፡

                                                         * * *

ሲልቪያ ፕላዝ እራሷን እንስቲቷ አልአዛር እያለች ነው የምትጠራው፤ ብዙ ጊዜ ከሞት ተርፋለች፤ ተነስታለች፡፡ እራሳቸውን ለማጥፋት ሞክረው የዳኑ ሠዎች ከሞት እንደተረፉ ሳይሆን ከሞት እንደተነሱ ነው የሚሰማቸው፡፡ የምናውቅ እናውቃለን፡፡ ሲልቪያ ፕላዝ Lady Lazarus በሚለው ግጥሟ ላይ እነኚህ ስንኞች አሉ፡- I have done it again One year in every ten I manage it… Soon, soon the flesh The grave cave ate will be At home on me --- I am only thirty And like the cat I have nine times to die. This is Number three What a trash To annihilate each decade --- The first time it happened I was ten It was an accident The second time I meant To last it out and not come back at all I rocked shut Dying Is an art, like everything else I do it exceptionally well. I do it so it feels like hell I do it so it feels real I guess you could say I’ve a call. ሲልቪያ ፕላዛ በአራተኛ የተሳካ ሙከራዋ፤ በ31 አመቷ ሞተች፡፡ ጠፋች፡፡

እራሷን አጠፋች፡፡ ምዕራፍ ሶስት፡- ዘመናዊው አጼ ቴዎድሮስ እንደተለመደው ጠዋት ከእንቅልፌ ነቃሁ፡፡ አምሽቼ ተኝቼ በጠዋት ነው የምነቃው፡፡ እንቅልፍ አይወደኝም፡፡ ለዚያም ይመስለኛል ሞት የሚጠላኝ። በሁለት ታክሲ ወደ ሰንጋተራ ሄድኩ፣ ወደ አረቄ ቤት፡፡ የአረቄ ቤት የጠዋት ጓደኛዬ አስፋው ቀድሞኛል፤ ቁርስ አብረን ነው የምንበላው፤ ማታ ማታ አስር አስር ብር አዋጥተን ለአረቄ ቤቱ ባለቤት እንሰጣለን፤ ጠዋት ጉበት ገዝቶ፤ ከትፎ፣ ቀምሞ ይጠብቀናል፤ አብረን እንበላለን፡፡ ዛሬ ሠኞ ነው፡፡ ሰኞ ይደብራል፡፡ (አጼ ቴዎድሮስ የሞተው ሰኞ ቀን ነው፤ በፋሲካ ማግስት፡፡) ዛሬ ሠኞ ነው፡፡ ዛሬ ቀፎኛል፡፡ (የዛሬው ቁርስ ከአስፋው ጋር የመጨረሻችን ይሆናል፤ አስፋው በንጋታው ይሞታል፡፡ አስፋውም ቀፎታል፡፡ በቅርቡ እንደሚሞት እንደታወቀው ያስታውቃል፡፡) ቁርሴን ከነ አስፋው ጋር በልቼ፣ አንድ አረቄ ጠጣሁ፡፡ አካሄዴ የተለመደ ነው፡፡ ጠዋት ቁርስ እበላለሁ፣ አረቄ እጠጣለሁ፣ ከዚያ ውሃ ያስፈልገኛል (ጠላ ወይ ድራፍት) ማለቴ ነው፡፡ ዛሬ ብር አለኝ፤ ድራፍት መጠጣት እችላለሁ፡፡

ወደ ቴሌ ባር ወረድኩ፡፡ በነገራችን ላይ በ dehydration እራስን ማጥፋት ይቻላል፤ በየእለቱ dehydrate የሚሆን ሰውነቴ ጠዋት ሁሌ ውሃ ይለኛል፡፡ ውሃ መጠጣት አልችልም፤ ጠላ እና ድራፍትን እንደውሃ ነው ሠውነቴ የሚጠቀማቸው፡፡ በ dehydration እራስን ማጥፋት ይቻላል፡፡ ከሰውነታችን ሰባ ከመቶው ውሃ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ አስራ አምስት በመቶ ብናጎል እንሞታለን፡፡ (ምናልባት ቀጣዩን ራሴን የማጥፋት ሙከራ የማደርገው በ dehydration ይሆን ይሆናል። ሌላም አማራጭ አለ፤ የከሰል ጭስ፤ ለምሳሌ ዘንድሮ ብቻ በከሰል ጭስ አዲስ አበባ ውስጥ አስራ አንድ ሰው ሞቷል፤ ስለዚህም አስብበታለሁ፡፡) ወደ ቴሌ ባር ሄደኩ፡፡ ውሃ ፍለጋ፡፡ የመጠጫ፣ የመጫወቻ፣ የመተከዣ፣ የመደንዘዣ፣ የማንበቢያ፣ የመፃፊያ ... የተለመደች ቦታ አለችኝ፡፡ እዚያ ቦታ ላይ ልቀመጥ ስል እልፍ ብሎ ያለው ወንበር ላይ ተአምር አየሁ፡፡ ውብ ሴት! ሌላ ገለፃ አያስፈልግም፡፡ ውብ ሴት፡፡

የተቆጣች ፀይም ውብ ሴት! ከሰው ጋር ናት፡፡ ወይ ከባሏ ጋር፣ ወይ ከጓደኛዋ ጋር፣ ወይ ከፍቅረኛዋ ጋር ናት፡፡ በሱ ነው የተቆጣችው፤ እሱን ነው የምትቆጣው፡፡ የተለመደ ቦታዬን ትቼ እነሱ አጠገብ ያለውን ወንበር ስስብ አንድ እጅ አብሮኝ ወንበሩን ሳበ፡፡ ሁለታችንም ልጅቷን እያየናት ስለነበር አልተያየንም፡፡ ወንበሩን አጥብቄ ያዝኩት። ልጅዬው በልመና አይነት አየኝ፡፡ በቁጣ አየሁት፡፡ አይኑን ቢያንከራትት ልጅቷ አጠገብ ምንም ወንበር የለም፡፡ ፈልጎ ሊያገኝ የቻለው ልጅቷ ፊት ለፊት ራቅ ብሎ ያለ ወንበር ነው፡፡ ወደዚያ አመራ፡፡ ከዚያ ትታየዋለች፤ ትርቅበታለች እንጂ ትታየዋለች፡፡

ልክ ልጅዬው ወንበሩን ለቅቆልኝ ሊሄድ ሲል፡- ልጅቷ እንዲህ ስትል ሰማናት፡- “እንዴት እንደዛ ታደርጋለህ;! የገዛ እህቴን;! እራሴ አልጋ ላይ;!” ወንበር እየተሻማኝ የነበረው ሰው ከርቀት ልጅቷን ሊያሳየው የሚችለው ወንበር ሊያዝበት ሲሆን እየሮጠ ሄደ፡፡ እውነት እሮጧል፡፡ “እህስ;” አለችኝ አለም አስተናጋጇ፤ የምንኖርባት አለም ብታስጠላኝም ይህቺ አስተናጋጇ አለም ግን ደስ ትለኛለች፤ እወዳታለሁ፡፡ “ድራፍት፡፡” አለም ድራፍቱን ልታመጣ ሄደች፡፡ ፊልም ላይም፣ መጽሄት ላይም፣ ምድር ላይም ይህችን የተቆጣች ጠይም የምትመስል ቆንጆ አይቼ አላውቅም፡፡ የተናገረችውን ስሰማ ግን ማመን አቃተኝ፡፡ አሁን የገረመኝ አብሯት ያለው ሠው ነው፤ እሷ አይደለችም፡፡ ምን አይነት ጀግና፣ ወይ ሠይጣን፣ ወይ መልአክ ቢሆን ነው ይህቺን ሴት ትቶ አልጋዋ ላይ እህቷን የሚዳራው;! አሁን ደግሞ አብሯት ቁጭ ብሎ እያወራ ነው፡፡ አየሁት፡፡ ግድየለሽ ነው፤ የእግዚአብሔር ግድ የለሽነት ይታይበታል፡፡ እያጨሰ ነው፤ እንደ ሰይጣን ነው የሚያጨሰው፡፡ (ይቀጥላል)

Published in ልብ-ወለድ

በ43 ሚሊየን ብር የቴክኖሎጂ ማስፋፊያ ሊሠራ ነው “የጉምሩክ አሰራር ቀልጣፋ አይደለም”

ለአገራችን እንግዳ ይሁን እንጂ በኤስያና በብዙ የአፍሪካ አገራት ታዋቂ ነው፡፡ በአፍሪካ፣ በናይጄሪያ፣ በታንዛንያ፣ በኮንጎ ኪንሳሻ፣ በሴኔጋልና በኬንያ፤ በኤስያ ደግሞ በሕንድ፣ በዱባይ፣ በሆንግኮንግ፣ በቪየትናም፣ … በአጠቃላይ በመላው ዓለም ከ20 አገሮች በላይ ቅርንጫፎች አሉት - ሞባይልና የተለያዩ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች አምራች የሆነው ጂኦቴል፡፡ መሠረቱ ቻይና ሸንዘን የሆነው ጂኦቴል፤ መካከለኛ ሞባይሎችን ዲዛይን እያደረገ የሚያመርት የኤሌክትሪክ ኩባንያ ነው፡፡ በኢትዮጵያ የተለያዩ ሞባይሎች ለመገጣጠም ሥራ የጀመረው በቅርቡ ነው - ባለፈው ዓመት ኅዳር ወር፡፡ “ተልዕኳችን፣ ለአጠቃቀም ቀላልና ምቹ፣ ከፍተኛ ጥራትና ተመጣጣኝ ዋጋ ያላቸው ሞባይሎች በማቅረብ በዓለም ዙሪያ የሚደረጉ ግንኙነቶችን ቀልጣፋና ተደራሽ ማድረግ ነው” ይላሉ፤ በኢትዮጵያ የጂኦቴል ሴልስ ማናጀር ሚ/ር ኮቢ፡፡ “የእኛ መርህ፤ ለብቻ መበልፀግ ሳይሆን ከአጋሮቻችን ጋር ማደግና የተሻለ ሕይወት መፍጠር ነው፡፡ ዓላማችን በመተባበር፣ በጋራ እምነት ላይ ተመሥርቶ ሰጥቶ መቀበል (win-win) ነው፡፡

 

ለስኬታችንና ለተወዳዳሪነት መሠረት የሆነን፣ ከማንም በላይ ለሰዎች ፈጠራ ትኩረትና እውቅና መስጠታችንና የአገር ውስጥ ጥሬ ሀብት መጠቀማችን ነው” ብለዋል፡፡ ሚ/ር ኮቢን በዚች አገር ኢንቨስት ለማድረግ ምን እንዳነሳሳቸው ጠየቅኋቸው፡፡ “ኢትዮጵያ ፈጣን ዕድገት እያስመዘገቡ ካሉና ነዳጅ አምራች ካልሆኑ 10 የዓለም አገራት አንዷ ናት። ወደ አገር ውስጥ የሚገባ ማንኛውም ካፒታልና እውቀት ኢኮኖሚውን ከፍ ያደርጋል፡፡ በዚህ ላይ ካፒታልና እውቀት ወደ ውስጥ የሚገባው በሁለት አቅጣጫ ነው፡፡ አንዱ ቻይናውያን ኢንቨስት የሚያደርጉት ነው፡፡ ሌላው ደግሞ በውጭ አገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ለዘመዶቻቸው የሚልኩት ከ1.5 ሚሊዮን በላይ ዶላር ነው፡፡ በዓለም ባንክ ሪፖርት መሠረት ባለፉት 10 ዓመታት ቻይናውያን ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ ኢንቨስት አድርገዋል። በውጭ አገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ደግሞ የአገሪቷን አጠቃላይ ምርት 10 በመቶ ወይም 3.2 ቢሊዮን ዶላር ያህል ወደ ኢኮኖሚው አስገብተዋል፡፡ “በኢትዮጵያ ከውጭ ወደ ኢኮኖሚው የሚገባውን ኢንቨስትመንት (ፎሬይን ዳይሬክት ኢንቨስትመንት) ከምርታማ ዕድገት ጋር ለማቆራኘት ያለው ዕድል ጠባብ ቢሆንም፣ መንግሥት፣ ሕዝብና ኢኮኖሚው፣ ዝግ ከሆነ ባህላዊ ኢኮኖሚ ተላቅቆ ፈጣን የሆነውን የዓለም ገበያ ይቀላቀላል የሚል እምነት አለን፡፡ እነዚህንና ሌሎች የዕድገት አማራጮችን በማጥናት ነው በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ የወሰነው” በማለት አብራርተዋል፡፡ ጂኦቴል በኢትዮጵያ እያደረገ ያለውን እንቅስቃሴ ያስረዱን፣ የጂኦቴል ባለቤት የሚ/ር ዣዥዋ አማካሪ አቶ ሰይፈ ስዩምና የማርኬቲንግ ኃላፊው አቶ አብዱልዓሊም አብደላ ናቸው። ጂኦቴል በኢትዮጵያ ሲመሠረት ካፒታሉ ምን ያህል ነው? አልኳቸው፡፡ አንድ ሚሊዮን 600ሺህ ብር ነበር፡፡

============

ምን ዓይነት ሞባይሎች ነው የምታመርቱት? በአሁኑ ወቅት ስማርት ፎን (ታብሌት) ወይም ሚኒ ኮምፒዩተር እና ተች ስክሪን ጨምሮ 22 ዓይነት የተለያዩ ሞባይሎች እናመርታለን፡፡ በአገር ውስጥ ከእኛ በስተቀር ስማርት ፎን የሚያመርት የለም። ስማርት ፎናችን እነ ጋላክሲ፣ አፕል፣ ሳምሰንግ፣ የሚጠቀሙበት አንድሮይድ የተባለ ፈጣን ሶፍትዌር የተገጠመለት ነው፡፡ ይህ ብቻም አይደለም፤ በጥራትና በዋጋም ደረጃ ቢሆን የደንበኞችን አቅም ያገናዘበ ነው፡፡ ስማርት ታብሌታችን ኮምፒዩተር ማለት ነው፤ ማንኛውም ኮምፒዩተር የሚሠራውን (ዎርድ፣ ኤክሴል …) ይሠራል፡፡ ዋጋው ምን ያህል ነው? ከ2500 እስከ 3000 ብር ነው፡፡ ደንበኞቻችን “ስማርት ፎንስ ጂኦቴል ይሥራ” እያሉ ስለሚያሞካሹን እንኮራበታለን፡፡ ይህ ሞባይል በከተማ አካባቢ ላሉ ለቴክኖሎጂ ቅርበት ላላቸውና ብዙ አፕሊኬሽን መጠቀም ለሚችሉ ደንበኞች የቀረበ ነው፡፡ በገጠር አካባቢ ላለው ኀብረተሰብስ? የመብራት አቅርቦት ዝቅተኛ በሆነባቸው ከከተማ ውጭ ላሉ የገጠር ተጠቃሚዎች በተመጣጣኝ ዋጋ፣ ጥራትና ረዥም የባትሪ ዕድሜ ያለው ሞባይል በአማራጭነት ማቅረባችን ተመራጭ አድርጐናል፡፡ ደንበኞቻችንም በዚህ ደስተኞች ስለሆኑ የሚሰጡን አስተያየት ጥሩና ለበለጠ ሥራ የሚያነሳሳ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት ምን ያህል ሞባይሎች ታመርታላችሁ? በዓመት 1.2 ሚሊዮን ሞባይሎችና 120ሺ ላፕቶፖች ለማምረት ነው ያቀድነው፡፡ ነገር ግን አሁን ጀማሪ ስለሆን ይህን ቁጥር አላሟላንም፤ የወደፊት ዕቅዳችን ነው፡፡

አሁን አንዳንድ ጊዜ በወር እስከ 5 ሺህ ሞባይሎች እናመርታለን፡፡ መገጣጣሚያዎቹን ከውጭ ስለምናስመጣ፣ የዶላር እጥረት፣ የዕቃዎቹ መዘግየት፣ … የመሳሰሉ ችግሮች አሉብን፡፡ በሙሉ አቅማችን ማምረት እስክንችል በዓመት እስከ 40ሺህ ሞባይሎች እናመርታለን፡፡ ላፕቶፕ ታመርታላችሁ እንዴ? አዎ! “አንድ ላፕ ቶፕ ለአንድ ተማሪ” በሚለው መርህ መሠረት፣ ወደ 43 ሚሊዮን ብር በሚጠጋ ገንዘብ በምንሠራው ማስፋፊያ፣ ላፕቶፖችን ለመሥራት ከኢንቨስትመንት ጽ/ቤት ፈቃድ ወስደን እየተዘጋጀን ነው፡፡ መቼ ነው ላፕቶፖቹን መገጣጠም የምትጀምሩት? በመጪው የፈረንጆች ዓመት መጀመሪያ ወይም በእኛ በጥር ወር ገጣጥመን በርካሽ ዋጋ ለማቅረብ ነው ያቀድነው፡፡ ርካሽ ስትሉ በስንት ብር? ዕቃዎቹን ከውጭ ስለምናስገባ በአምስትና በስድስት ሺህ ብር ለማቅረብ ነው ያቀድነው፡፡ ታዲያ ይኼ ርካሽ ዋጋ ያሰኛል? የተማሪዎችንስ አቅም ያገናዘበ ነው ትላላችሁ? እኛ አትራፊ ድርጅት ነን፡፡

ብዙም ባይሆን መጠነኛ ትርፍ ማግኘት አለብን፡፡ ትምህርት ሚኒስቴርና ሌሎች ድርጅቶች ድጋፍ የሚያደርጉልን ከሆነ ከዚህም በታች ዝቅ ባለ ዋጋ እናቀርባለን፡፡ በእርግጥ በመርህ ደረጃ አንድ ላፕ ቶፕ በ100 ዶላር ይቀርባል፡፡ በአሁን ወቅት የዶላር ምንዛሪ ደግሞ 2000 ብር ያህል ነው፡፡ ይህ በዕርዳታና በድጋፍ ሲሆን ነው፡፡ መገጣጠሚያ ዕቃዎቹ በውጭ ምንዛሪ ተገዝተው የሚመጡ ስለሆነ ውድ ናቸው፡፡ ድጋፍ ካላገኘን በስተቀር በዚህ ዋጋ ማቅረብ ይከብደናል፡፡ በጥር ወር ስማርት ፎንን ጨምሮ በወር አቅምን ያገናዘቡና ጥራት ያላቸው 100ሺ ሞባይሎችና በወር እስከ 30ሺ የሚደርሱ ላፕቶፖች ለማምረት አቅደናል፡፡ የአገር ውስጥ ፍላጐት ካረካን በኋላ ሞባይልና ላፕቶፖች ወደ ሱዳን፣ ላፕቶፕ ደግሞ ወደ ኬንያ በመላክ የውጭ ምንዛሪ በማምጣት በአገሪቱ ኢኮኖሚ ውስጥ ጉልህ ሚና ለመጫወት አቅደናል፡፡ አሁን በገበያ ውስጥ ያላችሁ ድርሻ ምን ያህል ነው? ጀማሪ እንደመሆናችን መጠን ከፍተኛ የሚባል አይደለም፡፡ ነገር ግን ገበያው ውስጥ መቆየት የሚያስችለን አቅም አለን፡፡ ከገበያው ውስጥ ምን ያህል ድርሻ ለመያዝ ነው ያቀዳችሁት? አዲስ በመሆናችን ያሰብነው ደረጃ ላይ አልደረስንም፡፡ በቅርብ ዓመት ውስጥ የአገሪቱ ቁጥር አንድ የሞባይልና የቴክኖሎጂ አቅራቢ ግሩፕ እንሆናለን፡፡

ጥገና መስጫ ማዕከል አላችሁ? መርካቶ አካባቢ ከይርጋ ኃይሌ የገበያ ማዕከል አጠገብ በተሠራው ሕንፃ በቅርቡ የጥገና አገልግሎት እንጀምራለን፡፡ ጥሩ እንቅስቃሴ ባለባቸው አካባቢዎች ደንበኞቻችን ወደ ዋናው የጥገና ማዕከል በመምጣት እንዳይጉላሉ፣ በአቅራቢያቸው ጥገና ቤቶች ከፍተን አገልግሎት ለመስጠት እንቅስቃሴ ጀምረናል፡፡ በዚህ የሞባይል መገጣጠም ሂደት ምን ችግር ገጠማችሁ? ችግሩን አሁን ነው እየተረዳን የመጣነው። ጉምሩክ አካባቢ የሚገባው ቃልና በተግባር የሚገለፀው የተለያየ ነው፡፡ በጉምሩክ ለምንከፍላቸው ታሪፎች፤ “ይለቀቃል” በሚል ታሳቢነት በዲፖዚት (ተቀማጭ) ነው የምናኖረው፡፡ ጉምሩክ ከውጭ የምናስገባቸውን የመገጣጠሚያ ዕቃዎች፣ በውጭ አገር ተገጣጥመው አልቆላቸው እንደሚገቡ ሞባይሎች እንጂ እዚህ እኛ እሴት ጨምረንባቸው እንደሚቀርቡ አያስብም፡፡ ስለዚህ ለዲፖዚት የተቀመጠውን ገንዘብ በታክስ ይወስደዋል እንጂ ታስቦ ቀሪው ተመላሽ አይደረግልንም፡፡

እንደዚህ ዓይነት ነገሮች ደግሞ ወጪያችንን በትክል እንዳናሰላ ችግር ይፈጥሩብናል። በዚህ አሠራር ላይ ቅሬታ በማቅረባችን “ከዚህ በኋላ እናስተካክላለን” ብለው ከቅርብ ቀን ወዲህ ከዲፖዚት ውጭ እንድናወጣ እየተደረገ ነው፡፡ ሌላው ደግሞ የጉምሩክ አሠራር ቀልጣፋ አይደለም። አሁን ጉምሩክ የሚያስከፍለው ቀረጥ በጣም ከፍተኛ ነው፡፡ ከውጭ ለመገጣጠም የምናስገባቸው ዕቃዎች፣ ያለቀላቸው ዕቃዎች በሚቀረጡበት ዋጋ ነው የሚቀረጡት፡፡ እኛ ብዙ ወጪዎች አሉብን፡፡ ለቤት ኪራይ ከፍለን፤ ለዜጎች የሥራ ዕድል ፈጥረን፣ ገቢ ዕቃ አስቀርተን፣ … የምንከፍለው ቀረጥ በጣም ከፍተኛ ነው - ተወዳዳሪ የሚያደርግ አይደለም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ የምናስመጣቸው ዕቃዎች (ለምሳሌ ሶፍትዌር) ጥራት ዝቅተኛ ይሆናል፡፡ በዚህ ጊዜ ዕቃዎቹን ወደመጡበት አገር ለመመለስ ችግር አለ፡፡ ጉምሩክ ለማስገባት እንጂ የገባውን ለማስወጣት ደንብ የለውም፡፡

እነዚህ ችግር ፈጣሪ ነገሮች ስለሆኑ መስተካከል አለባቸው፡፡ ምን ያህል ሠራተኞች አሏችሁ? ለጊዜው በአይቲ የሠለጠኑ 44 ሠራተኞች አሉን። ከተቀጠሩም በኋላ ሥልጠና እንሰጣቸዋለን። ከሌሎች ሞባይል መገጣጠሚያዎች የተሻለ ስለምንከፍል ከሌሎች ድርጅቶች ለቀው ወደ እኛ የሚመጡ ሠራተኞችም አሉ፡፡ በዚህም ሠራተኞቻችን ከእኛ ጋር ለመሥራት ደስተኞች ናቸው፡፡ ላፕቶፕ መገጣጠምና ሌሎች ማስፋፊያዎች ስንጀምር የሠራተኞቹ ቁጥር ከ80 እስከ 120 ይደርሳል፡፡ የወደፊት ዕቅዳችሁ ምንድነው? አሁን በኪራይ ቤት ነው የምንሠራው፡፡ በቅርብ ዓመት ውስጥ መሬት ወስደን የራሳችንን ፋብሪካ መገንባት ቀዳሚ ተግባራችን ነው፡፡ ከዚያም በሞባይልና በላፕቶፕ፣ በአጠቃላይ በኤሌክትሮኒክስ ምርት በአገሪቷ ቁጥር አንድ ተመራጭ ኩባንያ መሆን ነው፡፡ ከዚያም ምርቶቻችንን ወደ ውጭ አገራት በመላክ ለአገሪቷ የውጭ ምንዛሪ ማስገኘት ነው። የተለያዩ ብራንዶችን በመጠቀም ወደ ገበያው ለመግባትም እቅድ አለን፡፡

“የአገሬ ብርድ ግደለኝ፣ የአገሬ ፀሃይ ማረኝ፣ የአገሬ ዝናብ ደብድበኝ”

                    በአዲስ አበባም ሆነ ባብዛኛው የሀገራችን ክፍል ያለውን ያየር ፀባይ በዋዛ በማየት ተገቢውን ክብርና ዋጋ እንዳልሰጠነው ከተገነዘብኩ ቆየት ብያለሁ፡፡ ይህንን ግንዛቤዬን የበለጠ ያረጋገጠልኝ በቅርቡ ወደ አውሮፓ ያደረግሁት ጉዞ ነው፡፡ በየአመቱ በሚደረገው የፔን ዓለምአቀፍ ጉባዔ ተጋብዤ የአይስላንድ ዋና ከተማ ወደ ሆነችው ሬይኬቪክ መጓዜ የሀገሬ ብርድ ግደለኝ፤ የሀገሬ ፀሐይ ማረኝ፤ የሀገሬ ዝናብ ደብድበኝ ብዬ እንድመለስ አድርጐኛል፡፡ በሰሜን አትላንቲክ ውቅያኖስ የምትገኘው ትንሿ ደሴት በሰሜን አሜሪካና አውሮፓ መሀል ተሸጉጣለች። አብዛኞቹ ነዋሪዎች እንግሊዝኛ የሚናገሩ ቢሆንም አይስላንዶች የራሳቸው አይስላንዲክ ቋንቋ ይናገራሉ፡፡ ቋንቋቸውም ከእንግሊዝኛ ይልቅ ለስካንዲኒቪያን ቋንቋዎች የቀረበ ነው።

በሬይኬቪክ ዛፎች ለምልክት ካልሆነ በስተቀር የሉም ማለት ይቻላል፡፡ ለዘመናት በብርድ የተገረፈው ይህ አገር፣ ድንጋያማ ነው - በአለት የተሞላ፡፡ ኮረብታውም ሆነ ተራራው የገረጣና የጠየመ አለት ድንጋይ ነው፡፡ ሁለት መቶ ያህል እሳተገሞራዎች የፈነዱባት አይስላንድ፤ ብዙ ከአለት ሥር የተኙ ፍልውሃዎች ባለቤት ናት፡፡ ግሪን ላጐን እየተባለ የሚጠራውን ታዋቂ የፍልውሃ መዋኛን ጨምሮ ብዙ የፍልውሃ መዝናኛዎች፤ ፏፏቴዎችና ለአይን የሚማርኩ ወንዞች አሏት፡፡ የአይስላንድ ዋና ከተማ ሬይኬቪክ ስፋቷ በጣም ትንሽ ከመሆኑ የተነሳ አንድ ሰው ብርዱና ዝናቡ ካላወከው በቀር በ30 ደቂቃ ከጫፍ እስከ ጫፍ ሊያካልላት ይችላል፡፡

በሬይኬቪክ ብዙዎቹ ህንፃዎች ከአምስት ፎቅ የማይበልጡ ሲሆን ከተማው ውስጥ ዓይን የሚስበው ብቸኛ ህንፃ ወደጠፈር ለመብረር እንደተዘረጋ የህዋ ሰረገላ ወይም ክንፉን እንደጣለ ግዙፍ የአሞራ ቅርጽ የተሰራው ቤተክርስቲያን ብቻ ነው፡፡ ጠቅላላው የአይስላንድ ህዝብ ቁጥር ከሁለት መቶ ሃምሣ ሺህ አይበልጥም፡፡ የሀገሪቱ ኢኮኖሚም ከአሣ ማስገርና ወደ ውጭ መላክ ጋር እጅጉን የተቆራኘ ነው። የሀገሪቱ የኢኮኖሚ ደረጃ ከምዕራብ አውሮፓ ጋር የሚስተካከል ነው፡፡ ይሁንና አውሮፓዎችም ቢሆኑ ዘላቂ ህይወታቸውን በአይስላንድ ለመቀጠል የአየር ጠባዩ ስለሚፈታተናቸው የህዝቡ ቁጥር ከአመት አመት እጅግም ለማደግ አልተቻለውም፡፡

የአይስላንድ መንግስት ይህንን ተግዳሮት በመገንዘብ በተለይ ቱሪስቶች ከቀረጥ ነፃ የሚሆኑበትን መንገድ አመቻችቷል፡፡ ዘመናዊ የየብስ፤ የባህርና የአየር መጓጓዣዎች በመኖራቸው ቱሪስቶች በምቾት ወደፈለጉበት ሥፍራ እንዲጓጓዙ ሆኗል፡፡ በሬይኬቪክ ከተማ በጣም የገረመኝ ብዙ ቱሪስት ማየቴ ነው፡፡ አስቸጋሪ በሆነው የከተማዋ የአየር ፀባይ ይህንን ያህል ቱሪስት እንዴት ተገኘ? በዚህ በቁር ከተማ ይህንን ያህል ቱሪስት መምጣት ነበረበት? እያልኩ ከራሴ ጋር ሙግት መግጠሜ አልቀረም፡፡ እኔ ባረፍኩበት ፎስ ሆቴል የነበሩ የጀርመን፣ የፊንላንድና የአሜሪካ እንዲሁም ፋሮ አይላንድ ከተባለ አስገራሚ ሀገር የመጡ ቱሪስቶችን አናግሬያቸው ነበር፡፡ በመጀመርያ ከፋሮ አይላንድ የመጡ ሶስት ሴትና ሶስት ወንዶችን ሳናግራቸው “ፋሮ አይላንድ” የሚባል ሰምቼ ስላማላውቅ የት ነው ፋሮ አይላንድ ብዬ ስጠይቃቸው፣ ካርታ አወጡና ማሳየት ጀመሩ፡፡ በአውሮፓም ሆነ በሌሎች የሰለጠኑ ሀገሮች ለትንሹም ለትልቁም ካርታ እየመዘዙ አቅጣጫ ማመላከት የተለመደ ነው፡፡ ታዲያ አቅጣጫውን ሲያሳዩኝ ነጥብ የምታክል ደሴት ናት፡፡ በዙሪያዋ ዴንማርክ ስላለች “ከዴንማርክ ነው የመጣችሁት?” ስላቸው ፊታቸው ተቀያየረና “ከፋሮ ደሴት ነው የመጣነው” አሉ፡፡

ክሌር የተባለች መልኳ ከአውሮፓ ይልቅ ለአረቦች የቀረበ ሴት “ፌሮ ደሴት ከዴንማርክ ለመገንጠል የምትጥር ነች፡፡ ለጊዜው ግን በዴንማርክ አገዛዝ ስር ነን፡፡ የራሳችን ቋንቋና ባህል አለን” አለችኝ፤ ፈርጠም ብላ፡፡ እኔም ክሌርን አመስግኜ የፖለቲካ እሰጥ እገባ እንዳልፈለግሁ በመግለጽ እንዴት አይስላንድን የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ እንደመረጡ ጠየቅኋቸው፡፡ እነሱም ለሀገራቸው ቅርብ በመሆኗ፤ በቂ መረጃ በማግኘታቸውና ምቹ የአየር በረራ ስላላት እንደሆነ ገለፁልኝ፡፡ ከፌሮ ደሴት ቱሪስቶች ቀጥሎ ከጀርመን ሀምቡርግ የመጡትን ነበር የጠየቅኋቸው፡፡ ከሀምቡርግ የመጡትም ከበርሊን ወይም ፍራንክፈርት ይልቅ የኔዘርላንዷ አምስተርዳም እንደምትቀርባቸውና በ30 ደቂቃ ከሀምቡርግ ኔዘርላንድ እንደሚገቡ አጫወቱኝ፡፡ “ለምን አይስላንድን መረጣችሁ? ለምን ውቧን ኢትዮጵያ አትጐበኙም?” አልኳቸው፤ ትንሽ እያሳቅኋቸው፡፡ “ስለኢትዮጵያ ሰምተን አናውቅም፤ ስለ አይስላንድ በየመረጃ መረቡ፤ በቴሌቪዥኑ እናያለን፡፡ ሲመቸን መጣን፤ ሦስት አመት አጠራቅመን ነው የመጣነው፤ እስኪ ደግሞ ስለ ኢትዮጵያ እናጠናለን” አሉ፡፡ ከአሜሪካ የመጡት ቱሪስቶች ደግሞ “አይስላንድ የመጣነው ኪስ አውላቂ ሌባ እንኳ የሌለባት ፀጥተኛና ሰላማዊ ሀገር ስለሆነ ነው” ብለዋል፡፡

በነገራችን ላይ አይስላንድ የጦር ሰራዊት የላትም፤ ሌላ ቀርቶ የኔቶ የጦር መርከብና አየር ሃይል በሀገራቸው እንዳይንቀሳቀስ እየታገሉ ነው፡፡ በርግጥ ይህቺን ሚጢጢ ደሴት መጐብኘት እንደጀብዱ እንደሚቆጥሩትም አሜሪካኖቹ አልሸሸጉኝም፡፡ ሆነም ቀረ ምቹ የአየር ፀባይ ያላት ሀገራችን፤ ማንም ሰው ሳይሳቅቅ የሚጐበኛት ኢትዮጵያ፣ ለምን የሚገባትን ያህል ቱሪስቶች ለመሣብ አልቻለችም? እያልኩ ማሰቤን አላቋረጥኩም፡፡ አስቸጋሪ የአየር ፀባይ ያላትና ውድ የሆነችው ሬይኬቪክ ቱሪስት ከሳበች፣ ኢትዮጵያ የበለጠ ቱሪስት የማትስብበት ምክንያት አልታየኝም፡፡ በተለይ የአዲስ አበባ የአየር ጠባይ ብዙ ሊወራለት የሚገባ ሀብታችን ነው፡፡ ያረፍኩበት ሆቴል በባህር ዳርቻ አጠገብ ያለ ፎስ ሆቴል የሚባል እንደሆነ ጠቅሻለሁ፡፡ የተሰበሰብንበት አዳራሽ ደግሞ በከተማው ሌላ አይን የሚገባ ከክሪስታል የተሰራ የአራት መዐዘን ቅርፅ ያለው ዘመናዊ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ሲሆን ከሩቅ ሲመለከቱት የጠርሙስ ስብስብ ይመስላል፡፡

ሀርፖ የተባለው የመሰበሰቢያ አዳራሽ፤ ላቅና መጠቅ ያለ ጥበብ ይታይበታል፡፡ ይህንን የሰራው አርክቴክት ብዙ ሌሊቶችንና ቀናቶችን ያለ እንቅልፍ እንዳሳለፈ ብዙ ምልክቶች ትቷል፡፡ ከውስብስቡ የመስታወት ስራ ባሻገር ከአመት አመት ዝናብና ብርድ የማያጣውን የሬይኬቪክ ከተማ ብሩህና ምቹ ለማድረግ ብዙ ተለፍቶበታል፡፡ ካረፍኩበት ሆቴል እስከ መሰብሰቢያው አዳራሽ ቢበዛ የ10 ደቂቃ የእግር ጉዞ ነው፡፡ ታክሲ በጣም ውድ በመሆኑ የማይሞከር ነው፡፡ ለአውቶቡስ ደግሞ አጭር መንገድ ሆነ፡፡ በዚህ የተነሣ በእግራችን ማቅጠን የግድ ነበር፡፡ የ10 ደቂቃ የእግር ጉዞ ምን ችግር አለው ትሉ ይሆናል? በርግጥ በሀገራችን የአየር ጠባይ፣ በሸጋው አዲስ አበባ እንኳን 10 ደቂቃ ሌላም ቢሆን ችግር የለውም፡፡ ብርዱና ውሽንፍሩ እያፏጨ ጆሮ የሚበጥሰው፣ ፊት የሚገርፈው የሬይኬቪክ አየር ባለበት አንድ ደቂቃ ቀጥ ብሎ መራመድ ግን ፈተና ነው፡፡ ወይ አዲስ አበባ! ኧረ አየርሽ ይግደለኝ የሚያስብል ነው፡፡ አየር እየታሸገ ወደ ውጭ ሀገር የሚላክ ቢሆን ኖሮ፣ እንደ ኢትዮጵያ ሀብታም ሀገር ይኖር ይሆን? እንጃ? በጐበኘኋቸው ሀገራት ባብዛኛው ወይ ሙቀቱ ልብስ ያስጥላል ያለበለዚያ ብርዱ የተወለዱበትን ቀን ያስቆጥራል፡፡ የአዲስ አበባ አየር በብዙ መልኩ ሲታይ የተመጣጠነና ለኑሮ የተመቸ ነው፡፡ እርግጥ ነው በአይስላንድ ያለውን ከባድ ቅዝቃዜ ለመቋቋም ሙቀት ሰጪ ምግቦችን መብላት፤ ሙቀት ሰጪ የሆኑ ዘመናዊ ልብሶችን መልበስ የግድ ነው፡፡ ዘመናዊ ልብስ ያልኩት ብርድን ለመቋቋም ተብለው በልዩ ሁኔታ የተመረቱ ልብሶች በመኖራቸው ነው፡፡ ይሁንና ልብሱም ሆነ ምግቡ ውድ ነው፡፡ ለምሣሌ በአራት ጉርሻ የሚያልቅ ጥሩ ፒዛ አራት ሺ አይስላንድ ክሮነር ነው፡፡

ይህ ማለት ወደ ብር ስንቀይረው ወደ 750ብር ገደማ መሆኑ ነው፡፡ የሀገሩ የደሞዝ መጠን በአውሮፓ ደረጃ በመሆኑ ይህንን ከፍሎ መመገብ ብዙ አስቸጋሪ ላይሆን ይችላል ነገር ግን ምግቡም ሆነ መጠጡ ዋዛ እንዳልሆነ ለማሳየት ነው፡፡ በዚህ ላይ የተበላው ምግብ መቼ ከሆድ እንደሚጠፋ አይታወቅም፤ አሁን በልቶ አሁን አምጡ ያሰኛል፡፡ ብርዱ ብዙ ወጪን ያስከትላል፡፡ እንደ አዲስ አበባ ቤቶች ማሞቂያም ማቀዝቀዣም የሌላቸው ቤቶች የሉም፡፡ በሬይኬቪክ እያንዳንዱ ቤት ገና ሲሰራ ጀምሮ ማሞቂያ ይገጠምላቸዋል፡፡ በዚህ የተነሣ ከተማዋ ተጨማሪ የሀይል ፍላጐት ትጠይቃለች፡፡ ይህንን የሀይል (የሙቀት) ሂሣብ በመጨረሻ የሚከፍለው ነዋሪው ነው፡፡ በሀገራችን ያለው ሸጋው የአየር ፀባይ እንደ አሣማ ከመብላት እንዳዳነን የተገነዘብኩት እዚሁ ሬይኬቪክ ነው፡፡ ለጉባዔውና ለተሰብሳቢዎቹ ክብር የራት ግብዣ ተደርጐልን፣ ሆዳችን ቅሪላ እስኪያክል በልተን፤ አንዳንዶቻችንም ያለገደብ በቀረበው የወይን ጠጅ ሰክረን፣ ገና ከድግሱ አዳራሽ ወጥተን ጥቂት እንደተራመድን መብላት መጠጣታችን ተረስቶ ብርዱ ሆዳችን ገብቶ ያንሰፈስፈን ገባ፡፡ የበላነው ቡርንዶ አሣ፤ ሞቅ ያደረገን የወይን ጠጅን ብርዱ ይዞት ጠፋ!፡፡ ታዲያ በዚህ ሁኔታ እንኳን የሸመተ ያረሰስ ይችለዋል እንዴ? አወይ የአዲስ አበባ አየር መልካምነት! ውዱ የአዲስ አበባ አየርን እንደዋዛ እያየነው፣ እንደ እርጐ የሚገመጠውን የሸገር መዐዛ ያለውን የሀገራችንን ነፋስ መጠበቅ፤ መንከባከብ ችላ ያልነው ይመስለኛል፡፡ ልዩና ማራኪ የሆነው የሀገራችን የአየር ፀባይ፣ በተለይም የአዲስ አበባ አየር በምንም ሊለወጥ የማይችል ሀብታችን ነው፡፡ አሁን አሁን በእንጦጦ ተራራ ላይ ያለው የባህር ዛፍ እየሳሳ ነው፡፡ ከሩቅ ሲታይ ጥቅጥቅ ያለ ደን ይመስላል፤ ቀርበው ሲያዩት ግን መንምኗል፡፡ የአዲስ አበባ ምርጡ አየር ሚስጥሩ ይህ ደን በመሆኑ ተገቢ ጥበቃ ይሻል፡፡ በየአመቱ ሚሊዮን ዛፎች ቢተከሉም ዋናው መንከባከብ፤ ማሳደግ በመሆኑ የተተከሉት መፅደቃቸውንና ማደጋቸውን ማረጋገጥ ይኖርብናል፡፡ ግንባታዎችም ወደ ደኖቹ ዘልቀው ባይሄዱ መልካም ነው፡፡ በቸር ያቆየን፡፡

                 ባለፈው ረቡዕ ነው - የዘመን መለወጫ ዕለት፡፡ ሁዋዌ የተባለው የቻይና ቴክኖሎጂ ግሩፕ የኢትዮጵያ ቢሮ፣ ለክብረ አረጋውያን ምግባረ ሰናይ ድርጅት የተለያየ ቁሳቁስ ስጦታ ሲያበረክትና የምሳ ግብዣ ሲያደርግላቸው፣ ስጦታውን ከተረከቡት መካከል ሲ/ር ዘመናዊት ታዬ አንዷ ነበሩ፡፡ ሲ/ር ዘመናዊት ከአረጋውያኑ ጋር አብረው እየኖሩ በሙያቸው የመጀመሪያ ዕርዳታ ይሰጣሉ፡፡ ሲ/ር ዘመናዊት ቤታቸውን አንድ ሚሊዮን አንድ መቶ ሺህ ብር ሸጠው፣ ከአረጋውያኑ ጋር እየተጦሩ መሆኑን ሰማሁ፡፡ የሰማሁትን ማመን ከበደኝ፡፡ እውነት መሆኑን ለምን ከአንደበታቸው አልሰማም ብዬ አነጋገርኳቸው፡፡ የሰማሁት ነገር እውነት ነው፡፡ ሲ/ር ዘመናዊት አሁን የ76 ዓመት አረጋዊት ናቸው፡፡ ጎንደር ተወልደው እዚያው ነው ያደጉት፡፡ እስከ 8ኛ ክፍል ከተማሩ በኋላ አዲስ አበባ መጥተው የ2ኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በያኔው እቴጌ መነን፣ በዛሬው የካቲት 12 አጠቃላይና መሰናዶ ት/ቤት ተማሩ፡፡ 12ኛ ክፍል ሲያጠናቅቁ፣ ነርሲንግ ለመማር ልዕልት ፀሐይ ሆስፒታል (የዛሬው ጦር ኃይሎች ሆስፒታል) ገቡ፡፡

ተመርቀው ትንሽ እንደሠሩ፣ በ1952 ዓ.ም ከክቡር ዘበኛ ጦር ጋር ኮንጐ ዘመቱ፡፡ እዚያ አንድ ዓመት ቆይተው ሲመለሱ፣ ጦር ኃይሎች ሆስፒታል አንድ ዓመት ከሠሩ በኋላ አሜሪካ ሄዱ፡፡ አሜሪካ ዋሽንግተን ኮሎምቢያ ሆስፒታል ፎር ውመንስ በተባለ ሆስፒታል በሙያቸው ለአምስት ዓመት ሠርተዋል፡፡ በኢትዮጵያ አየር መንገድም ለሶስት ዓመት ሠርተዋል፡፡ ከአሜሪካ እንደተመለሱ በምኒልክ ሆስፒታል ለአንድ ዓመት ሠሩ፡፡ ከዚያም ወደ ቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ተዛውረው፣ ጡረታ እስከወጡበት ጊዜ ድረስ ለ25 ዓመታት ሠርተዋል፡፡ ሲ/ር ዘመናዊት፣ የረር አካባቢ በ280 ካ.ሜ ላይ ያረፈ ጥሩ ቤት ነበራቸው፡፡ ባለቤታቸው ሞተዋል፤ ልጆችም የላቸውም፡፡ ከወንድማቸው ልጅ ጋር ነበር የሚኖሩት፤ እሱም ሞተ፡፡ ከዚያ በኋላ ሁሉም ነገር ከንቱ ሆነባቸው፡፡

ለብዙ ጊዜ ካሰቡበት በኋላ በመጨረሻ ቤታቸውን ለክብረ አረጋውያን ምግባረ ሰናይ ድርጅት አወረሱ፡፡ በድርጅቱ ውስጥ ከአረጋውያን ጋር መኖር ከጀመሩ አንድ ዓመት ከአራት ወር ሆኗቸዋል፡፡ የድርጅቱ መሥራችና ዳይሬክተር ወ/ሮ ወርቅነሽ ሙኒኤ፤ ሲ/ር ዘመናዊት ያወረሷቸውን ቤት 1.1 ሚሊዮን ብር ሸጠው፣ የአዲስ አበባ መስተዳድር በሰጣቸው ቦታ ላይ ለአረጋውያኑ ቤት ሠርተው ከ15 ቀን በኋላ እንደሚገቡበት ገልጸዋል፡፡ “ሲ/ር ዘመናዊት ታዬ ትርፍ ቤት ሳይኖራቸው አንድ ቤታቸውን ለአረጋውያን በማውረሳቸው በጣም የማደንቃቸው ሴት ናቸው” ብለዋል፤ ወ/ሮ ወርቅነሽ።

Published in ህብረተሰብ

የአንበሶቹን ያህል ለሠራተኞቹ ጥንቃቄ አይደረግም - ሰራተኞቹ ቸልተኝነቱ ከቀጠለ ሌላም ሰው ሊሞት ይችላል - አስተያየት ሰጪዎች አደጋው የደረሰው አንበሶች በምግብ ስለተጐዱ አይደለም- ዋና ዳሬክተር ለአንበሳ ስጋ በዓመት ከ1.5ሚ ብር በላይ ወጪ ይደረጋል

             ባሳለፍነው ሰኞ ማለዳ ስድስት ኪሎ በሚገኘው አዲስ ዙ ፓርክ (አንበሳ ግቢ) ውስጥ በአንድ የግቢው ሰራተኛ ላይ የተከሰተው አስደንጋጭ አደጋና አሰቃቂ ህልፈተ ህይወት የብዙዎች መነጋገሪያ ሆኖ ሰንብቷል፡፡ በእለቱ ተራቸውን ጠብቀው የአንበሳውን ማደርያ ለማፅዳት ወደ ውስጥ የዘለቁት አቶ አበራ ሲሳይ የተባሉ ሰራተኛ፤ በጥቂት መዘነጋት አንበሳውን ወደ መዋያው አስገብተው በር ባለመዝጋታቸው፣ በአንበሳው ማጅራታቸውን ተይዘው፣ ለ20 ደቂቃ ያህል ሲሰቃዩ ቆይተው መሞታቸው እጅግ አሳዛኝ ክስተት መሆኑን የሟች ባልደረባ አቶ ምትኩ ጭብሳ ይናገራሉ፡፡

ምንም እንኳን አደጋው “በጥቂት መዘነጋት” እንደደረሰ ቢነገርም ይህ አይነት አደጋ የመጀመርያው እንዳልሆነና የመጨረሻውም ሊሆን እንደማይችል ነው የአንበሳ ግቢ ሠራተኞች የሚናገሩት፡፡ ከዚህ በፊት በአንበሳ ተበልተው የሞቱ አንድ ሰራተኛ እንደነበሩ የሚያስታውሱት ሰራተኞቹ፤ ተነክሰው ከሞት የተረፉም እንዳሉ ይገልፃሉ፡፡ አሁን ባለው ቸልተኝነት ከቀጠለም ሌላ ሰው መሞቱ አይቀርም ሲሉ ስጋታቸውን ተናግረዋል፡፡ በ1940 ዓ.ም ለቀዳማዊ ንጉሰ ነገስት ኃይለስላሴ፤ ከኢሊባቡር ጐሬና ከሲዳማ በመጡ አራት ትላልቅ እና ሶስት ደቦል አንበሶች የተመሰረተው አዲስ ዙ ፓርክ፤ ላለፉት 60 ዓመታት አንበሶችንና ሌሎች እንስሳትን አካቶ ለጐብኚዎች አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ ለንጉሱ የመጡት እነዚህ ሰባት አንበሶች በጊዜ ሂደት በመራባት በአሁኑ ሰዓት በፓርኩ ውስጥ የሚኖሩት አንበሶች ቁጥር 15 ደርሷል፡፡ ከነዚህ ውስጥ አምስቱ ሀይሌ፣ ቀነኒሳ፣ መሰረት፣ ጥሩነሽና እጅጋየሁ በሚሉ የታዋቂ ጀግኖች አትሌቶች ስም የተሰየሙ ሲሆን ሌሎቹም ላይሽ ተረፈ፣ ሰለሞን ጠንክር፣ መኮንን ተጋፋው፣ ወርቁ ገረመው፣ በሻዱ ጫላ፣ ቃኘው ወርቁ ወዘተ በሚል ስም ይጠራሉ፡፡ በተለይ ጠንክር የተባለው አንበሳ ከሁሉም አንጋፋው ሲሆን በ1984 ዓ.ም ነው የተወለደው፡፡

ቀነኒሳ በቀለ ወርቁ፣ ሀይሌ ገ/ስላሴ ወርቁና መሰረት ደፋር ወርቁ ወንድምና እህትና አንበሶች ናቸው፡፡ ወንድማማቾቹ ሀይሌና ቀነኒሳ በአንድ ማደሪያና መዋያ ቢያድጉም በጊዜ ሂደት ግን መስማማት አለመቻላቸው ብዙዎችን ያስጨንቅ እንደነበር የፓርኩ አስጐብኚ ይናገራሉ። በተለይ ቀነኒሳ ከወንድሙ ሀይሌ ጋር በየቀኑ መደባደብ ልማዱ ነበር፡፡ “በዚህም የተነሳ ሀይሌና ቀነኒሳን በተለያየ ኬጅ ውስጥ ለማዋልና ለማሳደር ግድ ሆኗል” ብለዋል - አቶ ምትኩ ጭብሳ። በነገራችን ላይ መጀመሪያ ከሞላ ጋር የመጣው ሉሉ የተባለው አንበሳ፤ በጃንሆይ የውሻ ስም የተሰየመ ሲሆን ሞላ የተባለው የመጀመርያው አንበሳም ሚስቱን በመግደሉ የሞት ፍርድ ተፈርዶበት እንደተገደለ ይነገራል፡፡ የአንበሶቹ አያያዝ በአሁኑ ወቅት በግቢው ውስጥ የሚኖሩት አንበሶች የሚመገቡት ስጋ በቀጥታ ከቄራ ተመርምሮ የሚመጣ ሲሆን ለእያንዳንዱ አንበሳ በቀን ከ5-7 ኪሎ ንፁህ ስጋ ይቀርባል፡፡ ለአንድ ኪሎ ስጋ 55 ብር ከ20 ሳንቲም እንደሚወጣና በቀን እስከ 120 ኪሎ የሚደርስ ንፁህና የተመረመረ ስጋ እንደሚቀርብ የፓርኩ ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ሙሴ ክፍሎም ተናግረዋል፡፡

አንበሶቹ በግቢው ውስጥ የራሳቸው ቋሚ ሀኪም ያላቸው ሲሆን ለውስጥ ጥገኛ ተውሳኮች ከምግብ ጋር መድሀኒት እንደሚሰጣቸውና ምርመራም እንደሚደረግላቸው ዋና ዳይሬክተሩ ገልፀውልናል፡፡ የአቶ አበራን በአንበሳው ተነክሶ መገደል ከአንበሶች በቂ ምግብ አለማግኘትና መጎሳቆል ጋር የሚያገናኙ ወገኖች እንዳሉ የተገለፀላቸው ዳይሬክተሩ፤ጉዳዩ መሰረተ ቢስ አሉባልታ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በአጠቃላይ አንበሶቹ በአመጋገብና በጤና በኩል አንዳችም ጉድለት እንደሌለባቸው የገለፁት ዶ/ር ሙሴ፤ አቶ አበራ ላይ የደረሰው አደጋ ከአንበሶቹ ምግብ ማጣትና ጉስቁልና ጋር እንደማይገናኝና አንበሶቹ በተፈጥሯቸው መላመድ የማይችሉ በመሆናቸው እንዲሁም በሩ ባለመዘጋቱና ከአንበሳው ጋር ፊት ለፊት ስለተገናኙ ለአሰቃቂው የህልፈት አደጋ መዳረጋቸውን አብራርተዋል፡፡ የአንበሶችን የምግብ አቅርቦት በተመለከተም፣ “የዚህ ፓርክ ትልቁ ወጪ የአንበሶች ምግብ ነው፤ በአመት ከ1.5 ሚሊዮን ብር በላይ ለስጋ ይወጣል።

ችግሩ የተፈጠረው አንበሳው ከማደሪያው ወደ መዋያው ከገባ በኋላ ሁለቱን ቦታዎች የሚያገናኘው በር ባለመዘጋቱ ነው፡፡ አንበሶች ምግብ አያገኙም ተጐሳቁለዋል እየተባለ የሚወራው ስህተት ነው” ብለዋል፡፡ ባለትዳርና የሶስት ልጆች አባት የነበሩት የ52 ዓመቱ አቶ አበራ ሲሳይ፤ ጠንካራና ታታሪ ሰራተኛ እንደነበሩ የጠቆሙት ዶ/ር ሙሴ፤ ወደ መጋቢነት እና ጽዳት ሰራተኝነት ከገቡ አንድ አመት ቢሆናቸውም በግቢው ውስጥ በሌላ የስራ ዘርፍ ለረጅም አመታት መስራታቸውን ተናግረዋል፡፡ “በዚህ ግቢ ውስጥ ሰው በአንበሶች ሲገደል የመጀመርያው አይደለም፤ ከዚህ ቀደም የተነከሰ ሠራተኛ አለ፤ ታዲያ ይህን ለመከላከል የዚህ ግቢ ሃላፊዎች ለምን ቅድመ ዝግጅት አያደርጉም?” ሲሉ ይጠይቃሉ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ አስተያየት ሰጪ፡፡ በዚህ ቸልተኝነት ከቀጠለ ሌላም ሰው ሊሞት እንደሚችል ስጋታቸውን የገለፁት ሌላው የፓርኩ ሰራተኛ፤ ለግንባታ ሰራተኞች ሄልሜት እና ሌላ የአደጋ መከላከያ መሳሪያዎች የሚሰጡ ሲሆን ለአንበሳ መጋቢዎችና ጽዳት ሰራተኞች ግን ምንም አይነት መከላከያ እንደሌለ ተናግረዋል። “ሌላው ቀርቶ የዋና ገንዳ ባለባቸው ቦታዎች ህይወት አድን ሰራተኛ (Life saver) ይዘጋጃል” ያሉት እኚሁ ሰራተኛ፤ አንበሳን ከሚያክል እንስሳ ጋር ለሚሰሩ ግን ምንም አይነት አደጋ መከላከያ እንደሌለ ገልፀው፣ ህይወት አድን ሰራተኛ ቢኖር ኖሮ ባልደረባቸው ከሞት ሊተርፉ ይችሉ እንደነበር በቁጭት ተናግረዋል፡፡

“ደሞዛችን እንኳን ከ600 ብር አይበልጥም፤ እኔ እዚህ ግቢ መስራት ከጀመርኩ 10 ዓመት አልፎኛል፤ ስራው ከባድ ክፍያው ግን አነስተኛ ነው” ያሉት ሌላው የግቢው ሰራተኛ፤ መንግስትና የፓርኩ ሃላፊዎች የሰራተኞችን ደህንነት ለመጠበቅ አስፈላጊውን ጥረት ማድረግና መሟላት ያለባቸውን ነገሮች በአስቸኳይ ማሟላት እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡ “ያለበለዚያ እኔ በአንበሳ ተንገላትቼ ስሞት ያየ ሌላ ሠራተኛ፣ ወደዚህ ግቢ ገብቶ ለመስራት እግሩን አያነሳም” ሲሉ ስጋታቸውን ገልፀዋል፡፡ የሰራተኞቹን የህይወት ዋስትና በተመለከተ የፓርኩ ዳይሬክተር ሲናገሩ፤ “ስራው ከባድና ከአንበሳ ጋር የሚሰራ እንደመሆኑ ሁሉም ሰራተኞች ኢንሹራንስ መግባት አለባቸው” ያሉ ሲሆን ይህንን ከግምት ውስጥ በማስገባት የኢንሹራንሱ ፕሮሰስ ተጀምሯል ብለዋል፡፡ “አንበሳውን ገድሎም ቢሆን የስራ ባልደረባችንን ለማዳን ጥረት ተደርጐ ነበር” ያሉት ዳይሬክተሩ፤ “ከዚያ በኋላ ሊመጡ የሚችሉትን አለም አቀፍ የእንስሳት መብት ጥያቄዎችና ሌሎች ጉዳዮችን እንመልሳቸው ነበር” ብለዋል፡፡ በፅዳትና በመጋቢነት ለሶስት አመታትን የሰሩት አቶ ምትኩ ጭብሳ፤ ከሌላ የስራ ዘርፍ ወደ መጋቢነት ሲዛወሩ የወሰዱት ስልጠና ስለመኖሩ ጠይቀናቸው፤ ስልጠና ሳይሆን በመ/ቤቱ የሚሰጡ መመሪያዎችና ማስጠንቀቂያዎች እንዳሉ ጠቁመው፤ ስራው ከአንበሳ ጋር የሚሰራና ህይወትን እስከማጣት ለሚያደርስ አደጋ የተጋለጠ በመሆኑ መዘናጋት እንደማያስፈልግ ተናግረዋል፡፡

“ሁሌም በአዕምሯችን ስጋት መመላለስ አለበት፤ በንቃትና በጥንቃቄ የሚሰራ ስራ ነው፤ ከአንበሶች ጋር የሚውል ሰው ለሰከንድ እንኳን መዘናጋት የለበትም” ሲሉም ምክራቸውን ይለግሳሉ፤ አቶ ምትኩ፡፡ በተለያዩ የአገር ውስጥ ሚዲያዎችና ድረገፆች የአቶ አበራ በአንበሳ መገደል ሲዘገብ የሰነበተ ሲሆን “ቀነኒሳ መጋቢውን ገደለ” የሚሉ እና መሰል አዘጋገቦችን በተመለከተ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጆርናሊዝም እና ኮሚዩኒኬሽን መምህር “አዘጋገቡ ከሙያ ስነ-ምግባር እጅግ ያፈነገጠ ነው፤ ታዋቂውን አትሌት ቀነኒሳንም የሚያስከፋና በመልካም ዝናው ላይ ጥቁር ነጥብ የሚጥል ነው” ሲሉ ተችተዋል፡፡ “በዚህ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን በሌሎች ፖለቲካዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ የሚዘገቡ በርካታ ዘገባዎች ሙያው ከሚፈቅዳቸው አካሄዶች ያፈነገጡ ናቸው” ያሉት መምህሩ፤ ሙያው በባህሪው ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሻ በመሆኑ ሙያተኞቹ ይህን ግምት ውስጥ በማስገባት መስራት እንዳለባቸው መክረዋል፡፡ ሌላው የግቢው ሰራተኛ የሆኑና ለ13 ዓመታት እንደሰሩ የገለፁ ግለሰብ “የአንበሶቹን ያህል ለእኛ ለሰዎች ጥንቃቄ አይደረግልንም” ያሉ ሲሆን የጓደኛቸው የአቶ አበራ አሟሟት ዘግናኝ እንደነበርና ነገ በራሳቸው ላይ ሊደርስ እንደሚችል ገልፀው፤ በጤና፣ በደሞዝና አደጋን በሚከላከሉ መሳሪያዎች ልንታገዝና መንግስት ከአቶ አበራ ሞት ትምህርት ወስዶ ሌሎች ሰራተኞችን ከአደጋ መታደግ አለበት ብለዋል፡፡

“ያለበለዚያ ግን አንበሶቹ ይወገዱ” ብለዋል - እኚሁ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ ሰራተኛ፡፡ የአንበሶቹ ዝርያ ለየት ያለ መሆኑ ከጀርመኑ “ላይፕ ዚክ” እህት ከተማ ጋር በመተባበር በተካሄደ የደም ምርመራ መረጋገጡን ዶ/ር ሙሴ ይናገራሉ። በኬጅ ውስጥ የሚኖር አንበሳ ከ20-25 ዓመት የመኖር እድል እንዳለው የገለፁት ባለሙያዎች፤ በዱር የሚኖር አንበሳ ግን በአማካኝ 14 ዓመት ብቻ በህይወት እንደሚቆይ ይናገራሉ፡፡ ምክንያቱን ሲያስረዱም በጫካ የሚኖር እንስሳ ምግብ ለማግኘት ብዙ ከመድከሙም በላይ ከሌሎች ጋር የሚያደርገው ተጋድሎ እድሜውን ያሳጥረዋል፡፡ በኬጅ የሚኖረው እድሜው የተሻለ የሚሆነው የተመረመረ ምግብ ከማግኘቱም በላይ ጤንነቱ በባለሙያ ክትትል ይደረግለታል፣ ከዚያም በላይ ከየትኛውም አቅጣጫ ትግልና ድካም አይኖርበትም ይላሉ- ባለሙያዎቹ፡፡ በአሁኑ ሰዓት በአዲስ ዙ ፓርክ ውስጥ 8 ወንድና ሴት አንበሶች፣ አምባራይሌ የተባለ እንስሳ፣ ጭላዳ ዝንጀሮ፣ ኤሊዎች፣ ንስር፣ ጦጣና የተለያዩ አዕዋፋት እንደሚኖሩም ለማወቅ ተችሏል፡፡

ባለፈው ሰኞ በአንበሳ ተነክሰው ለህልፈት የተዳረጉት ሟች አቶ አበራ ሲሳይ፤ ባለፈው ማክሰኞ በገርጂ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ስርዓተ ቀብራቸው ተፈፅሟል፡፡ ሰበተለያዩ የአገር ውስጥ ሚዲያዎችና ድረገፆች የአቶ አበራ በአንበሳ መገደል ሲዘገብ የሰነበተ ሲሆን “ቀነኒሳ መጋቢውን ገደለ” የሚሉ እና መሰል አዘጋገቦችን በተመለከተ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጆርናሊዝም እና ኮሚዩኒኬሽን መምህር “አዘጋገቡ ከሙያ ስነ-ምግባር እጅግ ያፈነገጠ ነው፤ ታዋቂውን አትሌት ቀነኒሳንም የሚያስከፋና በመልካም ዝናው ላይ ጥቁር ነጥብ የሚጥል ነው” ሲሉ ተችተዋል፡፡ “በዚህ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን በሌሎች ፖለቲካዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ የሚዘገቡ በርካታ ዘገባዎች ሙያው ከሚፈቅዳቸው አካሄዶች ያፈነገጡ ናቸው” ያሉት መምህሩ፤ ሙያው በባህሪው ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሻ በመሆኑ ሙያተኞቹ ይህን ግምት ውስጥ በማስገባት መስራት እንዳለባቸው መክረዋል፡፡

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 21 September 2013 10:37

የ“ሴቶች ለምን አይቀድሱም?”

ጥያቄ አልተመለሰም፤ አቶ መልካሙ ዳር ዳሩን አይዙሩ!

              “ሴቶች ለምን አይቀድሱም?” በሚል ርዕስ ነሐሴ 25 ቀን 2005 ዓ.ም በዚሁ ጋዜጣ ላይ ለወጣ ጽሑፌ “መልካሙ ተክሌ” እና “አንዱዓለም ናስር” የተባሉ ጸሐፊዎች መልስ ነው ያሉትን ፈጥነው በመላካቸው ላደንቃቸው እፈልጋለሁ፡፡ ሆኖም ሁለቱም ሰዎች ጳጉሜ 2 ቀን 2005 ዓ.ም በታተመው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ሲጽፉ ሃሳቤን የመደገፍም የመንቀፍም አዝማሚያ በማየቴ ጉዳዩ ጥርት ብሎ እስኪታወቅ ድረስ መጻፍ ያስፈልጋል ብዬ አመንሁ፡፡ አንባቢያን ግራ እንዳይጋቡ ሁለቱ ጸሐፊዎች ያተኮሩባቸውን ዋና ዋና ነጥቦች በየተራ እያነሳሁ መልስ ለመስጠት እሞክራለሁ፡፡ የአቶ መልካሙ ተክሌን ላስቀድም፡፡

አቶ መልካሙ ጽሑፋቸውን ሾርኔ በሚመስል ነገር ጀምረው የመጀመሪያዋ በደለኛ ሴትሔዋንመሆንዋን ሊነግሩን ሞክረዋል፡፡ ምንም እንኳ ይህን አባባል እስኪሰለቸን የሰማነውና የምንሰማው ዘወትራዊ ቃል ቢሆንም ይህን ጉዳይ በተመለከተ ደፈር ያሉ ጥያቄዎች ማንሳት ያስፈልጋል፡፡ የእውቀት መነሻ ጥያቄ ነዋ! [“አዳምና ሔዋን ተፈጠሩ” በተባለበት ወቅት ከሁለቱ ሌላ ሰብአዊ ፍጡር አልነበረም፡፡ እነሱም የተማሩ አልነበሩም፡፡ ታዲያ ሔዋን የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ መጣሷን ማን ቆሞ ተመልክቶ ነው እንዲህ ዘላለም ስትወቀስ የምትኖረው? ወንድ በነበረው አስተሳሰብ መሠረት ችግሮቹን ሁሉ በሴቶች ላይ የመጫን አባዜ ተጠናውቶት ይሆን ይህ አይነት አስተምሕሮ ሊቀጥል የቻለው? ኦሪት ዘፍጥረትን የጻፈውስ ማን ነው? ሴት ወይስ ወንድ? ወይስ ፈጣሪ ጻፈው? ሔዋን በደለች ብንል እንኳ ከአዳም ይልቅ እውቀትን ቀድማ የሻተች ናትና ልትወቀስ ይገባል? በእውቀት ላይ የተመሠረተ መልስ ያሻው ይመስለኛል፡፡ “ቅዱሳት ስለሆኑ፤ ሴቶች መቀደስ አለባቸው ብሎ መሟገት መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት የለውም” ሲሉም አቶ መልካሙ ሃሳቤን ለመተቸት ሞክረዋል። ግን መጽሐፍ ቅዱስ ሴቶች እንዳይቀድሱ የሚከለክልበትን ህግ አላሳዩንም፡፡

ያ ቢሆን ኖሮ በሌሎች የክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ ሁሉ ሴቶች እንዲቀድሱ አይፈቀድም ነበር፤ ለሃሳባቸው ክብደትም እጅ በነሳኋቸው ነበር፡፡ ግን ትችታቸው “ሾላ በድፍኑ” ሆነብኝ፡፡ እንዲያውም “ልክ መውለድ ለሴቶች እንደ ተሰጠ ሁሉ ቅዳሴ የወንዶች ድርሻ ነው፤ ቅዳሴ ተፈጥሯዊ የሥራ ክፍፍል ነው” ብለው የሌለና የማይመስል ነገር በጽሑፋቸው አስፍረዋል፡፡ እዚህ ላይ ነው አቶ መልካሙን “እንግባባ እንጂ” የምላቸው፤ አርግዞ መውለድንና ማገልገልን ምን አገናኛቸው? “ሕግን ያወጣው አምላከ እስራኤል እግዚብሔር እንጂ ሙሴ አይደለም” ሲሉም አቶ መልካሙ ለሙሴ ጥብቅና ለመቆም ሞክረዋል፡፡ በመሠረቱ እግዚብሔር ለሙሴ እንደሰጠው የሚታመነው አስርቱን ትእዛዛት ብቻ ነው - በጽላቱ ላይ ጽፎ የሰጠው፡፡ (ኦሪት ዘጸአት ምዕራፍ 20) ሕግጋቱን ሁሉ እግዚአብሔር ለሙሴ ሰጠው ብለን ብንቀበል እንኳ ዛሬ በፍጹም ተግባራዊ ሊሆኑ የማይችሉ ጉዳዮች እጅግ ብዙ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ባሪያ እንደ እንስሳት እንዲሸጥ እንዲለወጥ (ዘጸአት 21፡1-11) የሙሴ ሕግ ይፈቅድ ነበር፡፡ ይህ ለምን ሆነ ብሎ መከራከር አስፈላጊ አይሆንም፡፡

በጊዜው ሙሴ ሕግ አድርጐ አወጣው፤ እስከ 20ኛው መቶ ክ.ዘመን ድረስ ይህ ዘግናኝ ድርጊት በመላ ዓለም ተግባራዊ ሲሆን ቆይቷል፡፡ የማህበራዊ ህግጋት ባህርይ ከተፈጥሮ ህግጋት የሚለየው በሰዎች ተዘጋጅቶና ሥራ ላይ ውሎ መልሶ በሰዎች መሻሻል መቻሉ ነው፡፡ አንድ ሰብአዊ ሕግ ለሰዎች ህይወት ይጠቅማል ተብሎ ይዘጋጃል፤ እስከተወሰነ ጊዜ ሲያገለግል ይቆይና አላሰራ ሲል ይሻሻላል፤ ወይም ከነአካቴው ሊሰረዝ ይችላል። የተፈጥሮ ህግ ግን ዘለዓለማዊ ነው፡፡ የጨለማና ብርሃን፣ የሞትና ሕይወት፣ የክረምትና በጋ ወዘተ ህግጋት በሰው ሊሻሻሉ ወይም ሊቀየሩ አይችሉም፡፡ በመሆኑም የኦሪት ህግጋት የእግዚአብሔር ህግጋት ቢሆኑ ኖሮ፣ ዛሬም ሰው እንደ እንስሳት እንዲሸጥ፣ ዐይን ያጠፋ ዓይኑ እንዲጠፋ፣ የገደለ ሁሉ እንዲሞት፣ እናት አባቱን የሰደበ በሞት እንዲቀጣ፣ ዝሙት የፈፀመም በድንጋይ ተወግሮ እንደሚሞት አግባብ ነበር፡፡

እነዚህና መሰል ጉዳዮች ወንጀልነት ቢኖራቸውም ዛሬ ሙሴ ይቀጣበት በነበረው ዘግናኝ መንገድ አያስቀጡም፡፡ እንዲያውም እንደ ዝሙት ያሉት አንዳንድ ጉዳዮችማ የመንግሥታት እውቅና ሁሉ ተሰጥቷቸው የገቢ ማስገኛ እስከመሆን ደርሰዋል፡፡ ታዲያ አቶ መልካሙ ዛሬም የኦሪት ህግጋት ተግባራዊ መደረግ አለባቸው እያሉን ይሆን? መቸም በኦሪትኛ እንደማያስቡ እርግጠኛ ነኝ፡፡ “ቅዳሴ የመብትና የዲሞክራሲ ጉዳይ ሳይሆን የአገልግሎት ጉዳይ ነው” ሲሉም አቶ መልካሙ ድፍን ያለ መከራከሪያ አቅርበዋል፡፡ እኔ በመነሻ ጽሑፌ ላይ የገለጽሁት “ፍሬ ነገሬ ነገረ ሃይማኖት ነው” ብዬ ነበር፡፡ ምኑን ከምን ሊያነካኩት እንደፈለጉ ግልጽ አይደለም፡፡ ማነካካት ደግሞ ጤናማ መንገድ አይመስለኝም፡፡ ግን ወዳጄ ቅዳሴ የአገልግሎት ጉዳይ ከሆነ የእኔም ጥያቄ እኮ ይኸው ነው፡፡ ሊያገለግሉ ይችላሉ፤ በሌሎች አብያተክርስቲያንም እያገለገሉ ነው፤ እኛ አገርስ ለምን አያገለግሉም ነው፡፡

አቶ መልካሙ እንኳንስ የእኔን ጽሑፍ የራስዎንም ልብ አላሉትም እንጂ መጀመሪያ ላይኮ “ቅዳሴ የተፈጥሮ ድልድል ነው” ብለው ነበር፡፡ መልሰው ደግሞ “መብት አይደለም አገልግሎት ነው” አሉ፡፡ በእርስዎ ሃሳብ ለተወሰኑ ሴኮንዶች ልመራና መቀደስ የተፈጥሮ ስጦታ ከሆነ የመብት ጥያቄም ሊነሳ ግድ ይላል፡፡ ግን እነ አዳም “ልብሰ ተክህኖ ለብሰው ቀደሱ” የሚል ማስረጃ ሊያቀርቡ አይችሉም፡፡ ቅዳሴ የተጀመረውም ከክርስቶስ ልደት በኋላ ነው። ተፈጥሮአዊ ቢሆን ኖሮ ገና ድሮ ወይም ከፍጥረተ ሰብእ ጀምሮ መከናወን ነበረበት፡፡ “አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስራ ሁለት ሐዋርያት ሲመርጥ ሁሉም ወንዶች ነበሩ (ሐዋርያነት የጾታ ጉዳይ ባይሆንም) ሰላሳ ስድስት ቅዱሳት እንስትም መርጧል ከሴቶች” ሲሉ የሰጡት ሃሳብ ደግሞ ግራ ገብቶት ግራ የሚያጋባ ነው፡፡ አንዴ ሐዋርያት ወንዶች ነበሩ፤ እንደ ገና ደግሞ 36 ቅዱሳት አንስትንም መርጧል ብሎ ማደናገር ምን ይሉት ፈሊጥ ነው፡፡ “ቅዱሳት” መባላቸው የሚያሳየው ትልቅ ጉዳይ አለ፡፡ በኢየሱስ መመረጣቸውና ለሐዋርያዊ አገልግሎት ብቁ በመሆናቸው ነው፡፡

ታዲያ በኢየሱስ የተመረጡ መሆናቸውን የሚቀበሉ ከሆነ አቶ መልካሙ ሰው ሰራሹ ቤተ መቅደስ ነው ወይስ ኢየሱስ ይበልጥ ቅዱሱ? “ማርያም መቅደላዊት ረቡኒ (መምህር) ብላ ስትጠጋው … አትንኪኝ ብሏታል” ሲሉ የተረኩልን ጉዳይም የተዛባ ነው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ “ማርያም መግደላዊት” እንጂ “መቅደላዊት” አትባልም። መቅደላ ያለው እኛ አገር ደቡብ ወሎ ምዕራብ ወረዳዎች ውስጥ ነው፡፡ መግደላዊት የኖረችው ደግሞ ከገሊላ አካባቢ “መጌደል” ተብሎ በሚጠራው መንደር ነው፡፡ በመሠረቱ ማርያም መግደላዊት ከትንሣኤው በኋላ ከሐዋርያቱም ሆነ ከሌሎች ቅዱሳት አንስት ቀድሞ በአትክልት ቦታ- ኢየሱስ የተገለጠላት ቅድስት ሴት ናት፡፡ “አትንኪኝ” ያላትም ከማረጉ በፊት ማንም እንዳይነካው መለኮታዊ ሃይሉ ስለወሰነ እንጂ ማርያም መግደላዊት ቅድስና፣ ንጽህና ጐድሏት አይደለም፡፡ “ካልዳሰስሁ አላምንም” ያለው ቶማስ እጁ የተኮማተረውም ትዕዛዙን አላከብር ብሎ ነው፡፡

ስለሆነም ሴቶችም ሆኑ ወንዶች እንዳይነኩት ፈለገ ነው የሚባለው ወይስ “ሴቶችን ከልክሎ ለወንዶቹ ፈቀደ?” ክብደት ያጣ መከራከሪያ ነው፡፡ እስዋን ከልክሎ ቶማስ ቢዳስሰው ኖሮና በጤናው ቢቀር አባባልዎ ትክክል ሊሆን ይችል ነበር፡፡ በነገራችን ላይ አቶ መልካሙ የቅዳሴን ሥርዓት የደነገጉት ወንዶች ተሰብስበው እንጂ እግዚአብሔር ወይም እርስዎ እንዳሉት የተፈጥሮ ድልድል አይደለም። በአንድ ወቅት ስብሰባ ላይ የተቀመጡ ጳጳሳት፤ ከኢትዮጵያ ፓትርያርክ እንዳይሾም ህግ አቁመው ነበር፡፡ እስከ 1950ዎቹ ድረስ ይህ ህግ ተግባራዊ ሲደረግ ቆይቷል፤ ጳጳሳት ከግብጽ እየመጡ የሁከት ስራ ጭምር ሲያከናውኑ እንደነበር መገንዘብ ያለብዎ ይመስለኛል፡፡ ከኢትዮጵያ ጳጳስ እንዳይሾም የሚከለክለው ህግ በአባ ባስልዮስ ሹመት ምክንያት ውድቅ ተደርጓል፡፡

የቅዳሴ ሥርዓትም ልክ እንደ ፓትርያርክነቱ ሁሉ ሰው ሰራሽ ህግ ነው፡፡ ለዚህም ሲኖዶስንና ፍትሐ ነገሥቱን ቢያዩ እውነቱን ይገነዘቡታል፤ እንጂ በመጽሐፍ ቅዱስ ሴት እንዳትቀድስ የሚያግድ አንድም አንቀጽ አያገኙም ወዳጄ! “ኢየሱስ ምስጢረ መለኮቱን በደብረ ታቦር ሲገልጥ ሴቶች አልነበሩም” በማለት ሊያስረዱን የደከሙበት ነጥብም ጭብጥ አይሞላም፡፡ ደጋግሜ እንደገለጽሁት ትንሣኤውን ቅዱሳት አንስት እንዲያዩ ሲመረጡ አንድም ሐዋርያ አልነበረም፡፡ ታዲያ ሴቶች ከወንዶች ስለሚበልጡ? ወይስ ኢየሱስ ተአምራቱን ሊገልጥለት ለፈለገው ብቻ ስላደረገ? መከራከሪያዎን ደግመው ቢያዩት ከስሜት ይልቅ ሚዛናዊነት ጠቃሚ መሆኑን ሊገነዘቡ ይችላሉ፡፡

ከኢየሩሳሌም አጠገብ ከሚገኘውና “ቢታንያ” ተብሎ በሚታወቀው ቦታ ነዋሪ የነበረችው የማርታና የአልአዛር እህት ሌላዋ ማርያምንና ቤተሰቦችዋን ኢየሱስ ወደቤታቸው እየሄደ ይጠይቃቸው ነበር፡፡ ቃሉን ስለሰማችም ኢየሱስ አመስግኗታል (ሉቃስ 10፡39-42) ወንድሟ አልአዛር ከሙታን በተነሳ ጊዜም ከኢየሱስ ጋር በሰፊው ተነጋግራለች (ዮሐንስ 11)፡፡ ኢየሱስ እንደሚሞት ስለተረዳችና በጣም ትወደውም ስለነበር የናርዶስ ሽቱ እግሩን ቀባችው (ዮሐንስ 12፡1-8) የታናሹ ያዕቆብና የዮሳም እናት ማርያም ለክርስቶስ ስቅለትና መቀበር ምስክር ነበረች፡፡ (ማር. 15፡40-47፤ 16፡1፤ ሉቃስ 24፡10) ማርያም የቀለዮጳ ሚስትም ጌታ በተሰቀለ ጊዜ ከመስቀሉ አጠገብ ቆማ ነበር (ዮሐንስ 19፡25)፡፡ ሌሎችንም መጥቀስ ይቻላል፡፡ ስለሆነም አቶ መልካሙ ጌታ የፈቀደውን ያደርጋል እንጂ አንድን ተአምር ሲፈጽም የግድ የጾታ ስብጥር ያስፈልጋል አላለም፡፡ በደብረ ታቦር መለኮቱን ሲገልጥ ከነቢያትም ከሐዋርያትም ለተወሰኑት ታየ እንጂ ለጠቅላላው ነቢያትና ሐዋርያት አልተከሰተም፡፡

በኦሪት ዘመን ሐናን የመሰሉ በርካታ ሴት ነቢያት እንደነበሩም አይዘንጉ፤ “የእግዚአብሔር ወኪል ነበር” ያሉትን ሙሴን ከባህር ላይ አንስታ ያሳደገችው ሴት መሆኗንም አይዘንጉ፤ በቅዳሴ ሴቶቹን ማራቅ የተጀመረው ወንጌል ከተሰበከ ወዲህ ነው፡፡ “አንዱዓለም ናስር” የተባሉት ጸሐፊ ባነሷቸው ነጥቦች፤ በተለይ የወር አበባን አስመልክቶ ባቀረቧቸው መከራከሪያዎች ላይ በአብዛኛው እስማማለሁ፡፡ ሆኖም አንድ የዘለሉት ዋና ጉዳይ አለ። “ሴቶች ለምን አይቀድሱም?” ለተባለው ጥያቄ ቀጥ ያለ መልስ ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡ ልክ እንደ ወር አበባው ሁሉ ሴቶች ቢቀድሱ ምን ችግር (ካለ) ሊፈጠር እንደሚችል፤ ሳይንሳዊም ሆነ ሃይማኖታዊ ጥቅምና ጉዳት ካለውም እንዲሁ መረዳት እንችል ነበር፡፡ የሆነ ሆኖ የወር አበባ በኦሪት ዘመን የርኩሰት ምልክት እንደ ነበር ከክርስቶስ ልደት በኋላ ግን የርኩሰት ምልክትነቱ እንደ ቀረ፣ ሆኖም የወንዴ ዘር ካላገኘና የሚወጣ ከሆነ እድፍ እንደሚሆን የገለጹልን ጠቃሚ ሐሳብ ይመስለኛል፡፡ ግን የወር አበባ ጊዜያቸው ሳይደርስ፣ ወይም ከወር አበባቸው በኋላ ለምን አይቀድሱም? ርኩሰት አይደሉማ! እድፍ ከሆነ በውሃ ይነፃላ! እንወያይ፡፡

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 21 September 2013 10:34

የ‘ፌስቡክ’ ነገር…

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

ስሙኝማ…‘የፌስቡክ ሪቮሉሽን’ በአጠቃላይ ‘ፍሬንድ በፍሬንድ’ አደረገን አይደል! ወዳጅ እያጣን በእድርና እቁብ እንኳን መግባት ያቃተን ሁሉ ዕድሜ ለ‘ፌስቡክ’! ለምሳሌ አንዳንዱ፣ የሰፈሩ ህዝብ ሁሉ ልጆቹን ከእሱ ጋር እንዳይገጥሙ ስሙ እየተጠቀሰ ማስጠንቀቂያ የሚሰጥበት አይነት አለላችሁ፡፡ “አንተ ልጅ ከእሱ ጋር ትገጥምና ነግሬያለሁ። የስንት ሰዎችን ልጅ ያበላሸ ነው…” ወይም ደግሞ “አጠገቡ ድርሽ ትልና ውርድ ከራሴ፡፡ የእሱ ቤተሰቦቹ እንደሆኑ መተተኞች ናቸው፣ ልጄን ፉዞ እንዳያደርጉብኝ” ይባላል፡፡ እናላችሁ… ይህ የአምስት እድር ሰው በጠቅላላ… አለ አይደል… ‘እንትን የነካው እንጨት’ ያደረጉት ሰው በፌስቡክ ስንት ‘ፍሬንድስ’ ቢኖሩት ጥሩ ነው…ሦስት ሺህ አምስት መቶ! ይሄኔ እኮ በቱ ተዉአቸው፣ ድሮም ቢሆን ሀበሻ ምቀኛ፡፡

እኔ እንደሁ ሦስት ሺህ አምስት መቶ ፍሬንዶች አሉኝ…” ብሎ ቤተሰብ ጉባኤ ላይ ይፎክር ይሆናል፡፡ ደግሞላችሁ…ይቺ ‘ላይክ’ የምትባል ነገር አለች። እናላችሁ… “እግሮቿን አይቼ ነው የወደድኳት...” ብሎ ነገር የለ… “ቁመናው ደስ ሲል…” ብሎ ነገር የለ… (“እጥረቱ ደስ ሲል” የሚል የ‘ፌስቡክ ግሩፕ’ ሲቋቋም አስገቡኝማ!)…በቃ ‘ላይክ’ የምትለዋን ጠቅ በማድረግ ‘መውደድ’ ይቻላል፡፡ ታላላቆቹ መጻሕፍት ላይ ‘ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ… ምናምን የሚሉ ነገሮች አሉ። እናላችሁ…ዘንድሮ የመፋጠጥ ዘመን ሆነና…አለ አይደል… “እኛን ውደዱን ብሎ…” ነገር ፌስቡክ ያመጣብን ነው፡፡ (ያው “ላይክ አድርጉን” ማለት “ውደዱን…” ማለት ነው፡፡ አራት ነጥብ፡፡) እናላችሁ…የእኔ ቢጤዎች… አይደለም ሰዉ ተጠግቶ ወዳጅ ሊያደርገን…ቢተነኩሱት እንኳን የማይተነፍስ ‘ጭምት’ ውሻ ገና እንዳየን የሚጮህብን በሺህ የሚቆጠሩ ፍሬንዶች አሉን እላችኋለሁ፡፡

ደስ አይልም! እናላችሁ… ዘንድሮ የፌስቡክ ገጼን ‘ላይክ’ አድርጉ ማለት ያው በተዘዋዋሪ ‘ላይክ’ አድርጉኝ ማለት ነው፡፡ እናላችሁ… ‘መወደድ’ በማመልከቻ የሆነበት ፌስቡክ የማንወድሳ! ስሙኝማ….እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…እኔ እንደውም ወደፊት “የፌስቡክ ውሽምነት” በመጀመር ፌስቡክ ከተፈጠረ ጊዜ በኋላ (“ከሠላሳ አንድ ዓመት በኋላ…” እንደሚባለው…) የመጀመሪያዎቹ የምንሆን ይመስለኛል፡፡ ልክ ነዋ! ከዛማ… መቼም እኛ የያዝነው ነገር ሁሉ ‘ሲያልቅ አያምርብንም’ አይደል…በየቤቱ ፍልሚያው ይጀመራል፡፡ “አጅሬ በአንተ ቤት አልታወቀብህ መሰለህ፡፡ እንደው ዝም ብዬ ጫካ ውስጥ ምናምን የተፈጠርኩ ይመስልሀል!” “ምንድነው የምታወሪው?” “እባክህ ተወው…ደርሼበታለሁ ነው የምልህ!” “ምኑን ነው የምትደርሺበት?” “ፒያሳ ኢንተርኔት ካፌ ሆነህ ከፌስቡክ ውሽማሀ ጋር ምን ነበር ‘ቻት’ ስትደራረጉ የነበረው! በአንተ ቤት አታውቅብኝም ብለህ ነው፡፡” “በቃ…ስለ አንድ አዲስ የግጥም መጽሐፍ ነዋ…ሌላ ምን ‘ቻት’ አደረገ አሉሽ?” እናላችሁ…እዚህ አገር የማይሆን ነገር የለም፡፡

ደግሞላችሁ ሌላው አለ… “ስሚ… ይሄ ፌስቡክ ላይ ‘ቻት’ የምታደርጊው ሰውዬ ግን…ቢያርፍ አይሻለውም!” “የቱን ነው የምትለው?” “ያ ‘ፕሮፋይል ፒክቸሩ’ን ቢዮንሴ የሀበሻ ልብስ ለብሳ ያለችበትን ያደረገው…” “ታዲያ እሱ ምን አደረገ ነው የምትለው?” “ምንሽ ነው?” “የፌስቡክ ፍሬንዴ ነዋ!” “የፌስቡክ ውሽማዬ ብትይ አይሻልም!” “ማነው ደግሞ እንዲህ ያለህ?” “ብቻ… ማንነቱን ደርሼበት እንደ አዲስ አበባ መንገዶች ቆፍሬ፣ ቆፋፍሬ ገደል በገደል ሳላስመስለው አንፍሬንድ ብታደርጊው ይሻልሻል!” (ውሽማ ተብዬው ያለው እኮ ያለው ቱርክሜንስታን ሊሆን ይችላል! እናላችሁ…እንደውም አላማረብን…የፌስቡክ ውሽምነት ከተጀመረ ‘ትራጂ–ኮሜዲዎች’ የሚስማሙ መአት ታሪኮች ይኖራሉ፡፡ ስሙኝማ…ለምን ይዋሻል…እስካሁን ሀያ ‘ፌስቡክ ፍሬንድስ’ አሉኝ፡፡

ከእነሱም አንድ ስምንት፣ አሥሩ ሰሞኑን ‘አንፍሬንድ’ ይደረጋሉ፡፡ (እንትናዬ…ምን ያህል ‘ሻይ’ እንደሆንኩ በ‘ፌስቡክ ፍሬንዶቼ’ ብዛት አየሽ አይደል! እናማ… ዝምታ ማብዛቴ የፍላጎት አለመኖር እንዳልሆነ ግንዛቤ ይግባልኝማ! ቂ…ቂ…ቂ…) ለነገሩማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል……የ‘ፌስቡክ ኩኪንግ’ ምናምን አለ ይባላል፡፡ ግን እኮ አስቸጋሪ ነው፡፡ ልክ ነዋ… ለምሳሌ እሷዬዋ “ብረት መዝጊያ የሚሆን ተገኘ…” ትልና ያላትን ፎቶ ሁሉ ‘ሼር’ ታደርገዋለች፡፡ እናላችሁ… ቢዘገይም መቼም መጣላት አይቀርም አይደል… በእነዛው ኩክ በተደራረጉባቸው ‘ፌስቡክ’ ገጾቻቸው ላይ ይጣላሉ። እንግዲህ በእውነተኛው ዓለም ሲጣሉ “ፎቶዎቼን መልስልኝ…” ይባል የለ፡፡ ‘ፌስቡክ’ ላይ ሲጣሉ እሷ ምን የምትል ይመስለኛል መሰላችሁ… “‘ሼር’ ያደረኩህን ፎቶዎቼን ሁሉ ዲሊት አድርግልኝ!” ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ኮሚክ ዓለም እኮ ነች…ኦባማ ፑቲንን ‘አንፍሬንድ አደረጓቸው’ ሲባል በሳቅ አልተንፈራፈራችሁም! ለካስ… እነኚህ በ‘ሪሞት ኮንትሮል’ እጣ ፈንታችንን የሚወስኑት አንዳንዴ እንደ እኛ ያደረጋቸዋልና! እናላችሁ…‘ፌስቡክ’ ነገሮችን እየለወጠብን ነው፡፡ ደግሞላችሁ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ይቺ ‘ፕሮፋይል ፒክቸር’ የሚሏት ነገር አለች፡፡

…እንትና ‘ፕሮፋይል ፒክቸሩን’ ለውጧል ይባልና አዲስ የተለጠፈውን ስታዩት…ምን አለፋችሁ ግራ ነው የሚገባችሁ፡፡ አሀ…ልክ እሱን የሚመስል ቢያንስ በአሥራ ሰባት ዓመት የሚያንስው ወንድም እንዳለው አታውቁም ነበራ! ቂ…ቂ…ቂ… እናማ…የዚች ‘ከሠላሳ አንድ ዓመታት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ ያለፈች’ አገር ኑሮ እንኩሮ ያስመሰለው ሰው… ምን አለፋችሁ…ፌስቡክ ገጹ ላይ አበባ መስሎላችሁ ቁጭ፡፡ ዕድሜ ለፎቶሾፕ! (“አንዳንዴ ሳይህ ትራስ ከሆነ የምርጫ ዘመናት ያሳለፈ አሮጌ ካናቴራ ቢጤ ትመስላለሀ…” ብለህ በሞራሌ ጢብ፣ ጢብ የተጫወትከው ወዳጄ…በፎቶሾፕ ብራድ ፒትን ሆኜልህ ቁጭ ስል ምን እንደምትሆን ብቻ አይቼ! “ለዓይን አትሞላም…” “ፊትህ ምግብ አይበላም…” ምናምን ማለት የለ…በነገራችን ላይ “ቦይፍሬንድ ምናምን አይወጣላትም…” ያልከኝ ‘ሲሱ’ እዚሁ ነች!) የ‘ፌስቡክ ፕሮፋይል ፒክቸር’ ልጠፋ አሪፍነቱ ምን መሰላችሁ…“ከስድስት ወር ያልበለጠ ፎቶ…” የሚል መመሪያ አለመኖሩ! እናላችሁ… ፌስቡክ ነገሮችን ሁሉ እየለወጠብን ነው፡፡

ደግሞላችሁ… ‘ፋይንድ ፍሬንድስ’ የሚላችሁ ነገር አለ አይደል…“እንትና ሠላሳ ሰባት ‘ፍሬንድስ’ አግኝታለች…” ምናምን ይላል፡፡ ኮሚኩ ነገር እኮ “‘ፍሬንድስ’” አግኝቷል የሚባል ሰው ላገኘው ሰው እንደገና “‘ፍሬንድ’ እንሁን…” የሚል ጥያቄ ማቅረቡ። ደግሞላችሁ…‘ሼር’ መደራረግ የሚሏት ነገር አለችላችሁ፡፡ ይቺ አገር ከሠላሳ አንድ ዓመት በፊት… (ይሄ ነገር ደጋገመኝሳ! በ‘ናይጄርያ እጅ ላይ ስለጣሉን’ ይሆን እንዴ! ቂ…ቂ…ቂ…) ‘ሼር’ መደራራግ የ‘ፌስቡክ አካውንት’ አያስፈልገውም ነበር፡፡ “የጩኒ እናት እባክዎ አንድ ኩባያ ሹሮ ካለዎት…” “አቶ አስጨናቂ፣ እስቲ መጥረቢያህን አውሰኝ፣ ይሄ ዛፍ እኮ አስቸገረኝ…” ምናምን እየተባባለ ‘ሼር’ ይደራረግ ነበር፡፡ አሁን “‘ፌስቡክ’ን ክፈቺ ሼር ያደረግሁሽ ነገር አለ…” ምናምን ይባልና ሲከፈት ምን ቢሆን ጥሩ ነው… ማይሊ ሳይረስ ‘እንትኗን ገልባ’ ስትቀብጥ! እና ‘ፌስቡክ’ ብዙ ነገር እየለወጠብን ነው፡፡ ደህና ሰንበቱልኝማ!

Published in ባህል
Page 5 of 16