በሲሳይ መንግስቴ አዲሱና አለሙ ካሳ ረታ የተዘጋጀው በራያ ሕዝብ ላይ ያተኮረ መጽሐፍ ዛሬ እንደሚመረቅ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ “የራያ ሕዝብ የማንነት ጥያቄና የማእከላዊ መንግስታት ምላሽ፤ ከአጼ ዮሐንስ ፬ኛ እስከ ኢህአዴግ” በሚል ርእስ የተፃፈው መጽሐፍ የሚመረቀው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ በሚገኘው ራስ መኮንን አዳራሽ ነው፡፡

ፒያሳ አካባቢ የሚገኘውና ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በዓላትን ከነትውፊታዊ ይዘታቸው በማክበር የሚታወቀው ኤልቤት ሆቴል የ2006 ዓ.ም መጀመርያ ዐውደዓመትን ዋዜማ በባሕላዊ ይዘት እንደሚያከብር አስታወቀ፡፡ ከቀኑ 11 ሰዓት በመጀመር በሚቀርበው ዝግጅት ወጣቶች የባህል ልብስ ለብሰው “አበባየሆሽ” ብለው የሚዘፍኑበት ሲሆን የዘመን አቆጣጠርን አስመልክቶ ማብራሪያ በባለሙያ ይሰጣል፡፡ በዝግጅቱ የባሕል ዘፈኖች፣ ግጥሞችና መጣጥፍ እንደሚቀርቡና የችቦ ማብራት ሥነ ሥርአትም እንደሚኖር ይጠበቃል።

በደራሲ አለማየሁ ገላጋይ የተጻፈው ‘የብርሃን ፈለጎች’ የረጅም ልቦለድ መጽሃፍ ባለፈው ሰኞ ለንባብ በቃ፡፡ ከዚህ በፊት አጥቢያ፣ ቅበላ፣ ስብሃት ገብረ እግዚያብሄር - ህይወትና ክህሎት፣ ኩርቢት፣ የፍልስፍና አጽናፍና ኢህአዴግን እከስሳለሁ የተሰኙ መጽሃፍትን ለአንባብያን ያቀረበው ደራሲው፣ በቅርቡ ለንባብ የበቃውንና በደራሲ ስብሃት ገብረ እግዚያብሄር ዙሪያ የሚያጠነጥነውን ‘መልከዓ ስብሃት’ የተሰኘ መጽሃፍም በአርታኢነት አዘጋጅቷል፡፡
248 ገጾች ያሉትና ለደራሲው ስምንተኛ ስራው የሆነው የብርሃን ፈለጎች የረጅም ልቦለድ መጽሃፍ፣ በተለያዩ የመጽሃፍት መደብሮችና በአዟሪዎች በ45 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
ደራሲ አለማየሁ ገላጋይ በአዲስ አድማስና በሌሎች ጋዜጦች እንዲሁም መጽሄቶች ላይ ለረጅም አመታት የተለያዩ ስነጽሁፋዊ፣ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ጽሁፎችን በማቅረብ ይታወቃል፡፡

በ40 ዎቹ መጨረሻ ዕድሜዋ ላይ የምትገኘው አንጋፋዋ ድምፃዊ ሐመልማል አባተ፤ ሰሞኑን ዘጠነኛ አልበሟን ለጆሮ አብቅታለች፡፡ በአዲሱ አልበሟ ምን አዲስ ነገር ይዛ መጣች? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ሰላም ገረመው ከሐመልማል አባተ ጋር ተከታዩን ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡

ብዙ ጊዜ አልበም የምታወጪው የበአላት ሰሞን ነው፡፡ ይሄ በአጋጣሚ ነው ወይስ ሆን ብለሽ?
አጋጣሚ ነው፡፡ ከዚህ በፊት “አውደ አመት” የሚል ካሴት ለአዲስ አመት አውጥቼ ነበር፡፡ ከዛ በኋላ ሠው ሁልጊዜ ለአዲስ አመት ካሴት የማወጣ ይመስለዋል፡፡ እንደ አጋጣሚ ሆኖ የአሁኑም አልበሜ ሄዶ ሄዶ አዲስ አመት ጋ ደረሠ፡፡ በዚህ ደሞ ደስተኛ ነኝ፡፡
ከኮፒ ራይት ጥሰት ጋር በተገናኘ በቀዳሚነት “ካሴት አላወጣም” ያልሽው አንቺ ነሽ፡፡ ውሳኔሽ አልጐዳሽም?
እርግጥ አንድ ነገር ስትፈልጊ አንድ ነገር ታጫለሽ፡፡ በፊት የሚሠራው ከቨር ነበር፤ ከቨር ይሠራና ይላካል፡፡ በዚህ ጊዜ ሁሉም ሰው አንድ አይነት ጥራት ያለው ስራ አያገኝም፡፡ ምክንያቱም ሁሉም በራሱ ቴፕ ነበር የሚቀዳው፡፡ አንዳንዴ ክፍለ ሀገር ሔጄ የተቀዳውን ድምፄን ስሠማው፣ የህፃን ልጅ ድምፅ የሚመስልበት ጊዜ አለ፡፡ አንዳንድ ቦታ ደግሞ የወንድ ድምፅ ይመስላል፡፡ ያኔ ነው ውሳኔ ላይ የደረስኩት። “ከቨር የሚባል ነገር አይታተምም፤ ካሴቱ በፋብሪካ ነው የሚታተመው” ብዬ ወሠንኩ። ምክንያቱም ሠው የሚከፍለው ገንዘብ እኩል ነው፤ ግን የተለያየ ጥራት ነው የሚያገኘው። አሁን ካሴቱን እራሱ በፋብሪካ አሳትሜ ሁሉም ሠው አንድ አይነት ጥራት ያለው ሥራ እንዲያገኝ እየጣርኩ ነው። ለእኔ ምናልባት ሊጐዳኝ ይችላል፡፡ ቢሆንም ይሔንን ማድረግ የግድ ነው፡፡ በኮፒ ራይት ጥሰት ዙሪያ መንግስት መፍትሔ እንዲሰጠን ብዙ ጊዜ ጠይቀናል፡፡ ለረጅም ጊዜ ጠብቀናል፡፡ ህጉ ተፈፃሚ መሆን ነበረበት፡፡ ነገር ግን የኮፒራይት ጥሰት ፈጽመው የምናሳስራቸው ሠዎች ቶሎ ይፈታሉ፡፡ ይሄ ተገቢ አይደለም፡፡ አሁን ትንሽ ለውጥ እየታየ ነው፡፡ የሚመለከተው ወገን ለጉዳዩ ትኩረት ቢሠጠው እኮ አርቲስቱ ብቻ ሳይሆን ሁሉም ተጠቃሚ ነው፡፡ እኛ ሀብታም ስንሆን መንግስትም ሀብታም ይሆናል፡፡ እና አሁንም ተስፋ አንቆርጥም፡፡
የአሁን ዘመን ድምፃውያን በቴክኖሎጂ ይታገዛሉ። ይሄ ነገር ጥቅሙ ነው ጉዳቱ የሚያመዝነው?
ቴክኖሎጂ ጥቅም እንዳለው ሁሉ ጉዳትም አለው፡፡ የድሮ አሠራር አድካሚ ቢሆንም ደስ ይላል፡፡ ሁሉም ሙዚቀኛ እኩል አጥንቶ፣ እኩል ሠርቶ ቀጥታ ነበር የሚቀዳው፡፡ አንድ ዘፈን ሰርተን ሰርተን ሊያልቅ ሲል ከተሳሳትን፣ እንደገና ሀ ብለን ነበር የምንጀምረው፡፡ ግን ቀጥታ እየሠሙ መቀዳት በጣም ደስ የሚል ነገር አለው። አሁን ደግሞ ቴክኖሎጂው በጣም አግዞናል፡፡ ብሳሳት እዛችው የተሳሳትኩበት ቦታ ብቻ ነው የምንቀዳው። ግን ኦሪጅናሉን የድምፅ ቅላፄ እየወሠደው ነው። እርግጥ እንደ ድምፃዊው ችሎታ ይለያያል፡፡ ለምሳሌ ቴክኖሎጂ እንዳለ ሆኖ በጥንቃቄና በጥራት መስራት ይቻላል፡፡ ይሄ ግን በባለሙያው ብቃት ይወሰናል፡፡ አንዳንዴ የሚዘገንን ነገር እሠማለሁ፡፡ አንዴ ሰምተሽው ሆ ብሎ የሚጠፋ ነገር ይሆናል፡፡ እናም ቴክኖሎጂ ጥቅምም ጉዳትም አለው፡፡
በኮምፒውተር ታግዘው አልበም የሚያወጡ አርቲስቶች በተለይ መድረክ ላይ ያንኑ ድምጽ ለማውጣት ሲቸገሩ ይታያል…
ልክ ነው፤ ድምፅ ላይ በጣም ችግር ያመጣል። ለዚህ ነው በተፈጥሮ ድምፅ መቀዳት ያለብን። አንድ ዘፋኝ ያልሆነ ሠው የድምፅ ልምምድ በማድረግ ዘፋኝ መሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን በእነዚህ የኮምፒውተር ሲስተሞች ታግዞ ከሰራ እንደምናየው ነው፤ መድረክ ላይ ያስቸግራል፡፡
አልበም በማውጣት ረገድ ከአሁኑኑ ከድሮው አሰራር የትኛው ቀና ነው? ለአርቲስቱ ማለቴ ነው…
የመጀመሪያ ካሴቴ የወጣ ጊዜ እኮ እንደ አሜሪካ ሰለብሪቲ ነበር የምንሠራው፡፡ ሁሉም ነገር በአሳታሚው በኩል ነው የሚያልቅልሽ። አሁን ግን በኮፒራይት ጥሰት የተነሳ ነጋዴው ከስራው ወጥቷል፡፡ ያሉትም ቢሆኑም በጣም እየከበዳቸው ነው፡፡ ብዙ ብር ካወጡ በኋላ ስራው ኮፒ ስለሚሆን አይደፍሩትም፡፡ አሁን ትንሽ ለውጥ አለ፡፡ በ2006 ደግሞ የተሻለ ለውጥ ይመጣል ብዬ አስባለሁ፡፡ እስከዛው ግን በግላችን እየሞከርን ነው። አልበም ሲሰራ ብዙ ወጪዎች አሉ፡፡ አልበሙን ካስደመጥን በኋላ ከኮንሠርት እናገኛለን በሚል ነው የምንሰራው፡፡
እስቲ ስለአዲሱ አልበምሽ ንገሪኝ…ወጪውን፣ አሳታሚውንና ስለ ስራዎችሽ ይዘት…
አልበሜ መጠሪያው “ያደላል” የሚል ነው። ስያሜው ብዙ ትርጉም አለው፡፡ አርቲስቱን ቤቱ ቁጭ ብሎ የሚዘርፈውን የሚመለከት ሊሆን ይችላል፡፡ ሰሙ ደግሞ እግዚአብሔር በአምሳሉ ሲፈጥረን ለሠው አድልቷል የሚል ነው፡፡ ወርቁን እንደተፈለገ መተርጐም ይቻላል። በዚህ አልበም ሳይካተቱ የቀሩ ብዙ ትላልቅ ስራዎች አሉ፡፡ ሁሉም ነገር ሊወጣ ስለማይችል ያልተሠሩት ከተሠሩት በላይ አሉ። ለአዲሱ አልበሜ ብዙ ወጪ ነው ያወጣሁት፡፡ በዚህ አጋጣሚ መግለጽ የምፈልገው ካሴቱ ላይ ከተለመደው ውጭ ብዙ ስራዎች መካተታቸውን ነው፡፡ ሌላ ጊዜ የተለመደው ሲዲ ላይ ነበር፡፡ አሁን ግን ካሴቱን “C80” አድርጌ 16 ዘፈኖች ተካተውበታል፡፡ ሲዲው ላይ 14 ዘፈኖች አሉ፡፡ አሁን በአሜሪካ ካሴት ፋሽን ሆኗል፡፡ የእኛ አገር ሲዲ ጥራቱ ብዙም አይደለም፡፡ ስለዚህ ካሴቱን ተመራጭ አድርጌያለሁ፡፡ ሙዚቃውን ሙሉ በሙሉ ያቀናበረው አበጋዝ ነው፡፡ በግጥምና በዜማ አዳዲስ ደራሲዎችን አሳትፌያለሁ:- ምስክር አወል፣ ማስረሻ ተፈራ፣ የእኔው አካሉ፣ ፀጋዬ ስሜ (ጥሩ ጉራጊኛ ሠጥቶኛል) የሸዋ ኦሮሞ ባህላዊ ዘፈንም ሠርቼአለሁ። እስከዛሬ የሀረር ኦሮሞን ባህላዊ ዜማዎች ነበር የምሰራው፡፡ አሳታሚዋ እኔ ነኝ፡፡ ለዚህ ስራ ከ500ሺ ብር በላይ ወጪ አድርጌአለሁ። አከፋፋዩ ደግሞ ትልቅ ስም ያለው ሮማርዮ ሪከርድስ ነው። በጣም ቆንጆ ስራ ነው። አንድን ስራ እኔ ካላመንኩበት አላወጣውም፡፡ ያለዚያ እኮ በየአመቱ ካሴት አወጣ ነበር፡፡
ጳጉሜ 5 ለአዲስ ዓመት ዋዜማ በሚሊኒየም አዳራሽ ትዘፍኛለሽ፡፡ ዝግጅት ምን ይመስላል?
የምንችለውን ያህል እያደረግን ነው። ከአዳዲሶቹ ዘፈኖችም የተወሰኑትን እጫወታለሁ። በአዲስ አመት ያልተደሠተ ሰው አመቱን ሙሉ አይደሠትም ይባላል፡፡
በ2005 ዓ.ም በአገር ደረጃ ምን ለውጥ አስተውለሻል?
ሁሌም መጥፎ ጐን ብቻ ማውራት ጥሩ አይደለም፤ በጐ ጐንም መወራት አለበት። ለምሳሌ ከአሠራር ለውጥ ብንነሳ፣ የውልና ማስረጃ ቢሮ ትልቅ አርአያ ነው፡፡ ልክ እንደ ውጪ አገር ቁጥር እየሰጠ ነው የሚያስተናግደው፡፡ ያለ ወረፋው የሚገባ የለም፡፡ በዚህ ረገድ አቶ ይርጋን በጣም ማመስገን ነው የምፈልገው፡፡ ምክንያቱም ሌላ ቦታ እኛ ቁጭ ብለን ስንጠብቅ፣ ነጮች በቅድምያ ሲስተናገዱ ነው የምናየው። ቅር ያለኝ የቦሌ መንገድ ነው፡፡ እርግጥ ነው የቦሌ መንገድ በጣም አምሮበታል ፤ ነገር ግን ባለ ህንፃዎቹ ፓርኪንግ አለመስራታቸው እንዳለ ሆነ የፓርኪንግ ችግር ተፈጥሯል፡፡ እዚያ አካባቢ መኪና አቁሞ እቃ መግዛት አልተቻለም። ድሮ ቦሌ የሚታወቀው ካፌዎቹ በረንዳ ላይ ሠዎች ቁጭ ብለው ሲዝናኑ ነበር፡፡ አሁን ከሠኞ እስከ አርብ ጭር ብሎ ነው የሚውለው፡፡ ሌላው የመንገዶቹ አሠራሮችና የመብራት ሁኔታ አካል ጉዳተኛን ያማከለ አይደለም፡፡ እነሱም ዜጐች ናቸው፡፡ ይሄን ጉዳይ በተመለከተ ሁለት ቀን በግሌ መንገድ ትራንስፖርት ሄጄ ነበር፡፡ ግን የማናግረው ሰው ማግኘት አልቻልኩም፤ ስብሠባ ናቸው በሚል ምክንያት፡፡ በኪነጥበብ ዘርፍ ግን ምንም ለውጥ የለም፤ አርቲስቱ እየደከመ ነው ያለው፡፡ እኔ ውጪ ሀገር ሠርቼ የመጣሁትን ነው እየበላሁ ያለሁት እንጂ፤ ኪነ ጥበብ ቀዝቅዟል፡፡
በትርፍ ጊዜሽ ምን ትሰርያለሽ?
የቤት ስራ ያስደስተኛል፤ አበስላለሁ። አትክልቶችን እንከባከባለሁ፡፡ የሁለት ልጆች እናት ነኝ፡፡ ትልቋ ልጄ ማክዳ ትባላለች። በዚህ አመት ከአሜሪካ፣ ፖኖን ዩኒቨርስቲ ትመረቃለች፡፡ አሜሪካን አገር ጐበዝ ተማሪዎችን ለማበረታታት የምርቃት ሰርተፍኬታቸውን ፕሬዚዳንቱ ናቸው የሚሰጡት - በኋይት ሀውስ፡፡ የእኔም ልጅ ከክሊንተን፣ ከቡሽ እና ከኦባማ እጅ ወስዳለች። ይሔ ደስ ይላል፡፡ አሁን በአንትሮፖሎጂ ትመረቃለች፡፡ ከዚያ ወደ አገሯ መጥታ የመስራት ፍላጐት አላት፡፡
ሀመልማል ትዳር ትፈራለች እንዴ?
ምን ያስፈራል? እግዚአብሔር ላለለት ሠው በጣም ይመከራል፡፡ ከመጣ ደግሞ ሠርግ መደገስ ይቻላል፡፡ ልጆቼም አንዳንዴ ያሾፉብኛል፤ “እኛ ሚዜ እንሆናለን፤ አንቺ ደግሺ፤ ግን ባል የለም” ይሉኛል፡፡ አሁንም ከመጣ እሰየው ነው፡፡
ምን ዓይነት ሙዚቃዎችን ማድመጥ ትወጃለሽ?
ማናቸውንም የትዝታ ዘፈኖች አደምጣለሁ። ከበፊቶቹ ሙሉቀን ለእኔ ልዩ ነው፤ ከወጣት የጐሳዬን ዘፈኖች እወዳለሁ፡፡ ሁሉም ግን የራሱ የሆነ ጣዕም አለው፡፡
በ2005 ዓ.ም ያስደሰቱሽንና ያስከፉሽን ጉዳዮች ጥቀሺልኝ…
የጥበብ አጋራችን የነበረውን ድምፃዊ እዮብን ማጣታችን አሳዝኖኛል፡፡ የእዮብን መልካምነት ለማወቅ የቀብር ስነስርዓቱን መመልከት በቂ ነው፡፡ እንደ አንጋፋዎቹ ነው በበርካታ ህዝብ የተሸኘው፡፡ ሌላው በመብራት ሃይል ችግር ቤቴ ተቃጥሎ ነበር። ምንም እንኳን ራሱ መብራት ኃይል ቢሠራውም። እንደዚህ አይነት ስህተት እንዳይከሠት መብራት ሀይል ጥንቃቄ ማድረግ አለበት፡፡ ካሴቴ አልቆ ለ2006 አዲስ ዓመት መድረሱ ደግሞ በዓመቱ ካስደሰቱኝ ነገሮች ዋነኛው ነው፡፡
ሞሃ ለስላሳ እንዴት 500ሺህ ብር ስፖንሰር አደረገሽ?
ይሄ ገና ያልተሰራና ያልተጣራ ነገር ነው፤ ስለዚህ በዚህ ጉዳይ ላይ ምንም መናገር አልፈልግም፡፡
ቀጣይ ዕቅድሽ ምንድነው?
በሙዚቃው መገስገስ ነው የምፈልገው፤ከራሴ ስራ አልፌ የሌሎችን ፕሮዲዩስ ማድረግ እፈልጋለሁ። አመል ፕሮዳክሽን የተባለ ድርጅት አቋቁሜያለሁ፤ በዛ በኩል የሌሎችን ስራዎች ለማሳተም እቅድ አለኝ።
ለዋዜማ ኮንሰርት ምን ያህል ተከፈለሽ?
ይሄ የግል ጉዳይ ነው፤ መናገር ይከብዳል፤ ምክንያቱም እኔ እንደሌሎች ያልተከፈለኝን ተከፈለኝ ብዬ አጋንኜ ማውራት አልፈልግም፡፡ ከአዘጋጆቹም ጋር ጉዳዩ በግል እንዲያዝ ተነጋግረናል፡፡ ስለዚህ መናገሩ አስፈላጊ አይደለም፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 07 September 2013 11:24

የጉድ አውደ አመቶች!

አዲሱ አመት ከእሳት ጋር ሳይሆን ከሳቅ ጋር ----
ድንገተኛ ጩኸት… ያልተጠበቀ ዋይታ… ድብልቅልቅ ያለ እሪታ…
በ1997 ዓ.ም ወርሃ ጥር፡፡ ከወሩ ሌሊቶች በአንደኛዋ፡፡
መነሻው ያልታወቀ ጉድ፣ በእኩለ ሌሊት ከተፍ ብሎ የሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ዋና ግቢን አናወጠው። በእንቅልፍ እረፍትን ሊጎናጸፍ ወደየአልጋው የገባው፣ በየዶርሙና በየላይብረሪው መሽጎ ደብተሩ ላይ ያቀረቀረው፣ በጥበቃ ስራ ላይ የተሰማራው… ሁሉም በድንገተኛው ጩኸት ደነበረ፡፡
ተኝተው የነበሩ ደንብረው ተነሱ፡፡ ህልምን ከእውን በሚለየው ድንበር ላይ ቆመው በተምታታ ስሜት እየተርገፈገፉ ጠየቁ፡፡
“ምንድን ነው?”
“ማን ነው የሚጮኸው?”
“ምን ተፈጠረ?”
ሁሉም ግራ በመጋባት ይጠይቃል እንጂ፣ ለጥያቄው እርግጠኛ የሆነ ምላሽ የሚሰጠው አላገኘም፡፡ የደነገጠ ልብ የተረጋገጠ ምላሽ እስኪያገኝ አይጠብቅም፡፡ ይገምታል… መላ ይመታል…
እሳት… አውሬ… መደርመስ… እንዲህ ያለ ሌላ ሌላ አደጋ!
አንዳንድ እማኞች ጩኸቱ የመጣበትን አቅጣጫ ጠቆሙ፡፡ 308 ተብሎ ከሚጠራው የሴት ተማሪዎች የመኝታ ህንጻ አካባቢ አመለከቱ፡፡ ይሄን የሰሙም፣ በእሳት የሚጋይ ህንጻ በአይነ ህሊናቸው እየታያቸው ወደዚያው ጎረፉ፡፡
ጩኸቱ ግን እንደተባለው ከ308 ህንጻ ብቻ አይደለም የሚሰማው፡፡ ከየአቅጣጫው ነው የሚደመጠው፡፡ እዚህም እዚያም እሪታ ሆነ፡፡ የሆነ ቦታ ላይ በሆነ ሰበብ የጀመረው ጩኸት፣ ስጋትና ጭንቀት የወለደው ሌላ ጩኸትን እየፈጠረ ዙሪያ ገባውን አናወጠው፡፡
የዩኒቨርሲቲው ግቢ በእኩለ ሌሊት በዋይታ ተደበላለቀ፡፡ ጨለማ ውስጥ ሽብር ነገሰ፡፡ ሁሉም በጭንቅ ተውጦ ተተራመሰ፡፡
ሁሉም በድንጋጤና በፍርሃት እየተንቀጠቀጠ፣ ከወዲያ ወዲህ ተራወጠ፡፡ ምድረ ተማሪ የመጣውን ጉድ ለማየት ይሁን ከመጣው ጉድ ለማምለጥ በማይለይ መልኩ ደመነፍሱ ወደመራው አቅጣጫ ሮጠ፡፡
ጩኸቱ ከዩኒቨርሲቲው ግቢ አልፎ፣ ባሻገር ወዳለው መንደር ዘልቆ፣ ወደ ከተማዋ ተሻግሮ ተሰማ፡፡ ከተራራ እስከ ተራራ…ከታቦር እስከ አላሙራ፣ ከመንደር እስከ መንደር… ከሰፈረ ሰላም እስከ አረብ ሰፈር ዙሪያውን ይሰማ ጀመር፡፡ ይሄን የውድቅት ዋይታ የሰማው የአዋሳ ህዝብ፣ ተማሪው በሆነ አደጋ ከመጥፋቱ በፊት ፈጥኖ ደርሶ ሊታደገው ወደ ግቢው ተመመ፡፡
ፈጥኖ ደራሽ ፖሊሶችን የጫኑ መኪኖች ሳይረናቸውን እያሰሙ፣ በተሸከርካሪ መብራት ጨለማውን እየከተፉ ወደ ግቢው ከነፉ፡፡ ከውጭም ከውስጥም ጭንቅና ትርምስ ሆነ፡፡ ከብዙ ግርግርና ትርምስ፣ ከብዙ ድብልቅልቅና ውዥንብር፣ ከብዙ ስጋትና ፍርሃት በኋላ… ተማሪው ለማምለጥና ለመዳን፣ ፖሊስና ህዝቡ ለመድረስና ለማዳን በጨለማ ውስጥ ትንፋሽ እስኪያጥራቸው ከሮጡ በኋላ… ድንገት የጀመረው ጩኸት፣ ድንገት ቆመ፡፡
“ምንድን ነው ነገሩ?” የሚለው የብዙዎች ጥያቄ ምላሽ አገኘ፡፡
“የኒው ይር ሴሌብሬሽን ነው!” ተባለ፡፡
ይህቺ ናት ‘ኒው ይር ሴሌብሬሽን’!!... በሰው ድግስ አስረሽምቺው!!...
ሁሉም የሰማውን ለማመን ተቸገረ፡፡ እርግጥ ነው፡፡ የፈረንጆች አዲስ አመት የጠባው ከደቂቃዎች በፊት ነው፡፡ ይህቺን ሌሊት በጉጉት ሲጠብቁ የከረሙ፣ ወር ሳምንት… ቀን ሰዓት… ደቂቃና ሰከንድ ሲቆጥሩ የቆዩ፣ በአገራቸው ሆነው የሰው አገር ዘመን መለወጥ ያስፈነደቃቸው የአንድ ዶርም ‘ሞደርን ተማሪዎች’ ነበሩ ጩኸቱን የጀመሩት፡፡
የ‘ሞደርኖቹ’ የ‘ሴሌብሬሽን’ ጩኸት ከዶርም ዶርም፣ ከህንጻ ህንጻ እንደሰደድ እሳት እየተዛመተ፣ ብዙዎችን በፍርሃት ካንቀጠቀጠ፣ ፖሊስን ካተራመሰ፣ የአዋሳን ህዝብ ካላቀሰ በኋላ ተቋጨ!! የአዲስ አመት መጥባትን ምክንያት በማድረግ የተፈጠረ ጩኸት መሆኑ የተነገራቸው አንዳንዶች፣ በነገሩ ግራ ተጋቡ፡፡
“ደሞ በጥር የምን አዲስ አመት መጣ?” በማለት ጠየቁ፡፡
“የፈረንጆች አዲስ አመት ዛሬ ነው የሚገባው” የሚለው ማብራሪያም አላረካቸውም፡፡
“ታዲያ እነሱን በፈረንጅ አውዳመት ምን ጥልቅ አረጋቸው?... ቢሆንስ ደሞ፣ አመት በአል በጩኸት ነው እንዴ የሚከበረው?” አሉ በንዴትና በግራ መጋባት፡፡
እርግጥ ይህን ጩኸት ያሰሙት የአዋሳ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች መሆናቸው ቀርቶ አየርላንዳውያን ቢሆኑ ኖሮነ ነገርዬው እምብዛም ባላስገረመ ነበር፡፡ ምክንያቱም በዓሉ በዓላቸው፣ ጩኸቱም ባህላቸው ነውና!! አየርላንዳውያን የአዲስ አመትን አከባበር የሚጀምሩት፣ በዋዜማው ምሽት በየቤታቸው ግድግዳና በር ላይ ዳቦ በማንጠልጠል ነው፡፡ ዳቦው የተትረፈረፈ ጸጋን እንደሚስብና መጥፎ መንፈስንና ክፉ እድልን ከቤታቸው እንደሚያስወጣ ያምናሉ፡፡ በዚህም አያበቁም፡፡ ከቤታቸው በዳቦ ያባረሩት መጥፎ መንፈስና ክፉ እድል ከደጃፍ እንዳይጠብቃቸው በመስጋት በእኩለ ሌሊት ከቤታቸው ይወጣሉ፡፡ ጆሮ የሚበጥስ ሃይለኛ ጩኸትም ያሰማሉ፡፡
ሁሉም በየደጃፉ ቆሞ አቅሙ በፈቀደው መጠን እሪታውን ያቀልጠዋል፡፡ ህጻን አዋቂው ጉሮሮው እስኪደርቅ በመጮህ፣ ከደጃፉ ያደፈጠውን መጥፎ መንፈስና ክፉ እድል ከአገር ምድሩ ጠራርጎ ያስወጣና፣ አዲስ አመትን “በል እንግዲህ ሰተት ብለህ ግባ!!” ብሎ ይቀበላል፡፡
የአዲስ አመትን መምጣትና የዘመንን መለወጥ እንዲህ በአስገራሚ አኳኋን የሚያከብሩ አገራትን ህዝቦች ተሞክሮ በጥቂቱ እንካችሁ…
አንዲት ብራዚላዊት የወርቅና የአልማዝ ጌጣጌጦቿን አወላልቃ ወደ ባህር ስትወረውር ቢያዩ፣ ጤንነቷን ሊጠራጠሩ ይችላሉ፡፡ አይጠራጠሩ! ጤነኛ ናት፡፡ ጌጣጌጦቿን ወደ ባህር የምትወረውረውም፣ ያለፈውን አመት በሰላም በጤና እንዳሳለፈችው ሁሉ፣ አዲሱ አመትም የሰላምና የጤና እንዲሆንላት አምላኳን ለመለመን ነው፡፡
ኮፓካባና ተብሎ የሚጠራው የብራዚል ባህር ዳርቻ፣ አመቱን ሙሉ በቱሪስቶች የሚጥለቀለቅ ታዋቂ የመዝናኛ ስፍራ ነው፡፡ ኮፓካባና ከአመት አመት የመዝናኛ፣ ከአመት አንድ ቀን ደግሞ የአውዳመት የማክበሪያና የመማጸኛ ባህር ነው፡፡ ብራዚላውያን በዘመን መለወጫ ዋዜማ በሚያከናውኑት ‘ፌስታ ዲ ኢማንጃ’ የተባለ ባህላዊ ክብረበዓል፣ ወደ ባህሩ አቅንተው ‘ኢማንጃ’ የተባለችዋን የባህር አምላክ ይለማመናሉ፡፡ አዲሱን አመት መልካም እንድታደርጋቸው ይጸልያሉ፡፡ በስተመጨረሻም ወደ ባህሩ እጅ መንሻ ይወረውራሉ፡፡ በአዲስ አመት ዋዜማ ወደ ባህሩ የሚወረወሩት ጌጣጌጦች ብቻም አይደሉም፡፡ ውድ ዋጋ የሚያወጡ ሽቶዎች፣ አበቦችና ፍራፍሬዎች ጭምር እንጂ፡፡
ወደ አገራችን መጥቶ በጥምቀት በኣል የታደመ እንግዳ ዴንማርካዊ፣ ኮበሌው ወደ ልጃገረዷ ደረት ሎሚ ሲወረውርና ጡቷን ሲመታ ቢያይ ግራ ሊጋባ ይችላል፡፡ ውርወራው ፍቅር መግለጫ እንደሆነ አያውቅምና፡፡ ወደ ዴንማርክ አቅንቶ የዘመን መለወጫ በዓላቸውን የታደመ የኛ አገር ሰው በተራው ፣ ስኒ እንደ ድንጋይ ወደየቤቱ ደጃፍ ሲወረወር ቢያይ በተመሳሳይ ግራ መጋባቱ አይቀርም፡፡ ውርወራው ፍቅር መግለጫ እንደሆነ አያውቅምና፡፡
ዴንማርካውያን በአዲስ አመት ዋዜማ እኩለ ሌሊት ላይ፣ የማጀት እቃዎቻቸውን ለቃቅመው ወደ ጎዳና ይወጣሉ፡፡
በጨለማ ውስጥ ተደብቀው ወደመረጡት ጎረቤት ወይም ወዳጅ ዘመድ ቤት በማምራትም የማጀት እቃዎቻቸውን እንደ ድንጋይ ይወረውራሉ፡፡ በዚህች ምሽት ብርጭቆ፣ ትሪ፣ ሰሃን፣ ጭልፋ፣ ማንኪያ፣ ድስትና ሌላ ሌላው የቤትእቃ በሙሉ ከየመደርደሪያው ወርዶ ወደየቤቱ ደጃፍ ይወረወራል፡፡ ከግድግዳ እየተጋጨ፣ ከመስኮት እየተፋጨ፣ በየበሩ ሲሰባበር፣ በየደጃፉ ሲነካክት ያመሻል፡፡
ንጋት ላይ… ሁሉም ከቤቱ በመውጣት በየራሱ ደጃፍ የተጠራቀመውን ስብርባሪ የማጀት እቃ በማየት ደስታን ይጎናጸፋል፡፡ የተሰባበረው እቃ የመልካም ነገሮች ምሳሌት ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ምሽቱን ወደቤቱ ብዙ እቃ ሲወረወርበት ያደረ፣ሲነጋ ከደጃፉ ብዙ ስብርባሪ ተጠራቅሞ ያገኘ ቤተሰብ፣ በሌሎች ዘንድ የበለጠ ተወዳጅ እንደሆነና መጪው አመትም በተለየ ሁኔታ የደስታ፣ የብልጽግናና የጤና እንደሚሆንለት ይታሰባል፡፡ ዴንማርካውያን ከዚህ በተጨማሪም በአዲሱ አመት ዋዜማ እኩለ ሌሊት ላይ፣ ወንበር የመዝለል ባህል አላቸው፡፡ ይህም ከአሮጌው አመት ወደ አዲሱ አመት፣ ከችግር ወደ ስኬት በሰላማዊ ሁኔታ የመሸጋገር ተምሳሌት ተደርጎ ይወሰዳል፡፡
“ቺሊያውያን የዘመን መለወጫን በዓል ከዘመድ አዝማድ ጋር ነው የሚያከብሩት” ብዬ ስነግርዎት፣ “ታዲያ ይሄ ምን ይገርማል?… እኛስ ከዘመድ አዝማድ ጋር አይደል እንዴ የምናከብረው?!” እንደሚሉኝ አውቃለሁ፡፡
ነገሩ ወዲህ ነው…
የቺሊያውያንን የዘመን መለወጫን በዓል ከዘመድ አዝማድ ጋር የማክበር ባህል ከኛ የሚለየው ዋናው ነጥብ፣ ወደዘመዶቻቸው የሚሄዱት በዋዜማው ምሽት መሆኑ አይደለም፡፡ በህይወት ወዳሉ ዘመዶቻቸው አለመሄዳቸው እንጂ!! ቺሊያውያኑ በዋዜማው ምሽት በሞት የተለዩዋቸው ዘመዶቻቸው ወዳረፉበት መካነ መቃብር ያመራሉ፡፡ በድቅድቅ ጨለማ በተዋጠው መቃብር ውስጥ አረፍ ብለውም፣ ካረፉ ዘመዶቻቸው ጋር በዓሉን በዝምታ ጨዋታ ሞቅ ደመቅ አድርገው ያከብራሉ፡፡
አዲሱ አመት የሰላም፣ የደስታና የብልጽግና እንዲሆንላቸው የሚመኙ የላቲን አሜሪካ አገራት ዜጎች ደግሞ፣ በዋዜማው ምሽት ቀይ ወይም ቢጫ የውስጥ ሱሪ የማድረግ ልማድ አላቸው፡፡ ቀዩ ለብልጽግና፣ ቢጫው ደግሞ ለፍቅርና ለሰመረ ትዳር ይመረጣል፡፡
በአዲስ አመት ጥሩ ፍቅርና የሰመረ ትዳርን ስለመሻት ካነሳን አይቀር፣ የአየርላንዳውያን ሴቶች ልማድ እንመልከት፡፡ በአዲሱ አመት ጥሩ ፍቅርና የሰመረ ትዳር ይገጥማት ዘንድ የምትመኝ አየርላንዳዊት ሴት፣ በበዓሉ ዋዜማ ሚስትሌቶ የሚባል የተክል አይነት በትራሷ ስር ሸጉጣ ታድራለች፡፡
በአገራችን ስራ ተፈትቶና ዘና ተብሎ የሚከበረው የዘመን መለወጫ በዓል፣ በኮሎምቢያና በሜክሲኮ ከዋዜማው እኩለ ሌሊት አንስቶ ከባድ ሸክም በመሸከም እንደሚከበር ሲሰሙ ምን ይሉ ይሆን?
የአሮጌው አመት የመጨረሻ ዕለት ተጠናቅቃ የአዲሱ አመት የመጀመሪያ ቀን ስትጠባ፣ ስኮትላንዳውያን ቤተሰቦች ማልደው በር በሩን ማየት ይጀምራሉ፡፡ ቀጣዩ የበዓል አከባበር የሚደምቀውና የሚሞቀውም ሆነ የቤተሰቡ የአዲስ አመት እጣፈንታ የሚወሰነው በጠዋት ነው፡፡ በዚህች ማለዳ ቀድሞ ወደ ቤታቸው የሚመጣው ሰው ነው ሁሉንም የሚወስነው፡፡
ደጃፋቸውን ቀድሞ የረገጠው ሰው፣ ቁመተ ሎጋና መልከመልካም ወንድ ከሆነ ደስታ ነው፡፡ እሱ የአዲሱ አመት መልካም እድል ምልክት ነው፡፡ ቀይ ጸጉር ያላት ሴት አልያም ህጻን ልጅ ከሆነ ደግሞ አመቱ ለቤተሰቡ ይዞት የሚመጣው አንዳች መከራ አለ ተብሎ ይታመናል፡፡
የሚመጣውን አዲስ አመት ወደቤታቸው በሚመጣው ሰው የሚተነብዩት ስኮትላንዳውያን ወንዶች፣ የዘመን መለወጫ በአልን በአጉል ጨዋታ ነው የሚያከብሩት - በእሳት እየተጫወቱ፡፡ ነበልባል እሳት እንደ ኳስ እያንጠባጠቡና በሰራ አካላቸው ላይ እያሽከረከሩ በመንገድ ላይ እየተደሰቱ በመጓዝ፡፡
አዲሱ አመት ከእሳት ጋር ሳይሆን ከሳቅ ጋር እየተደሰቱ የሚጓዙበት ይሁንልዎት!!

 

 

Published in ጥበብ

አዲስ አድማስ ጋዜጣ ለዚህ ስላበቃኝ ልዩ ትዝታ አለኝ
*እነፕሮፌሰር መስፍንና ፕሮፌሰር አስራት ደንበኞቼ ነበሩ
*የጋዜጣ አዟሪነት ሥራዬ አንባቢ እንድሆን አድርጎኛል

ከሊስትሮነት አንስቶ ሲዲ እስከማዞር ሥራ ላይ የተሰማራው ወጣት ተስፋዬ ፈጠነ፤ ለበርካታ ዓመታት ጋዜጣ ሲያዟር እነ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያምና ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ደንበኞቹ እንደነበሩ ይናገራል፡፡ ጋዜጣ አዟሪነቱ አንባቢ እንዳደረገው የሚገልፀው ወጣቱ፤አሁን ወደ ፊልም አከፋፋይነት ገብቷል፡፡
የአማርኛ ፊልሞችን እየገዛም በዲቪዲ እያወጣ ይሸጣል፡፡ በቅርቡ የራሱን ፊልም ለማውጣት እየሰራ መሆኑን ከሚናገረው ወጣት ተስፋዬ ፈጠነ ጋር የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ መልካሙ ተክሌ አጭር ቆይታ አድርጓል፡፡

እስቲ ራስህን አስተዋውቅ----
ተስፋዬ ፈጠነ እባላለሁ፡፡ ፊልም አሳታሚ ነኝ፡፡ ከጐጃም ሙዚቃ ቤት ጋር ነው የምሰራው። የራሴን ድርጅትም ከፍቻለሁ፤ “ፒያሳ ዘ አራዳ ኢንተርቴይመንት” ይባላል፡፡ ሲኒማ የማሳተም ፍቃድ ነው ያወጣሁት፡፡ መሸጥ የሚፈልጉ ባለፊልሞች ሲኖሩ እየገዛሁ አሳያለሁ፡፡ ብዙ ፊልሞች እኔ ጋ ይመጣሉ፡፡ መርጬ ከእነሲኒማ ቤቱ መግዛት ካለብኝ ከእነሲኒማ ቤቱ እገዛለሁ፡፡ የሲኒማ ቤት ጊዜውን ጨርሶ የመጣውን ደግሞ በቪሲዲ ወይም ዲቪዲ አሳትማለሁ፡፡
“አዲስ አድማስ”ን ጨምሮ ሌሎች ጋዜጦችን ታዞር ነበር፡፡ እስቲ ስለእሱ ንገረኝ…
ሥራዬን በፍቅር ነበር የምወደው፡፡ በ1985 ዓ.ም ነው ማዞር የጀመርኩት፡፡ እነ ጦቢያ፣ እነ ሪፖርተር ሲጀመሩ ትዝ ይለኛል፡፡ ሊስትሮ እየሰራሁ ጋዜጣ አዞር ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ አዲስ አድማስ መጣ፡፡ እነ እንዳልክ ሲያከፋፍሉ፣ ፒያሳ አካባቢ እኔና አንድ ልጅ ነበርን ጋዜጣ የምናዞረው፡፡ ከቲሩም ፒያሳ እኔ፣ ኤንሪኮ እና ቶሞካ አካባቢ ደግሞ እንግዳው የሚባል ልጅ ያዞር ነበር፡፡
አራት ኪሎ እነ ጥላሁን ያዞሩ ነበር፡፡ አዲስ አድማስ ተመስርቶ እስከ አስረኛው እትም ድረስ እኔ ነበርኩ እየዞርኩ ማስታወቂያ እለጥፍ የነበረው። ትንሽ ቤት በ60 ብር ተከራይተን ማስታወቂያውን እያባዛን በየቦታው እንለጥፍ ነበር፡፡
አዲስ አድማስ ሲጀመር ገበያው እንዴት ነበር?
እስከ ረፋዱ አራት ሰዓት ሸጬ እጨርስ ነበር፡፡ አንባቢዎች የት የት እንደሚገኙ አውቃለሁ፡፡ አራት መቶና አምስት መቶ ጋዜጣ እሸጣለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ነፃ ነኝ፡፡
ከሰዓት በኋላ ወደ ሊስትሮዬ እመጣለሁ። ጀብሎ እሰራለሁ፡፡ አዲስ አድማስን በተመለከተ ግንኙነቴ ከእንዳልክ ጋር ነበር፡፡ ጋዜጣው አለቀ ተብለን አዟሪዎች የምንጣላበት ጊዜ ነበር፡፡
የተለዩ አንባቢዎች ነበሩህ?
በጣም ታዋቂ ደንበኞች ነበሩኝ፡፡ ይረሱት ይሆናል እንጂ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ደንበኛዬ ነበሩ፡፡ ሟቹ ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስም ደንበኛዬ ነበሩ፣ ሊሴ ጀርባ ወደነበረው ቢሮአቸው እወስድላቸው ነበር፡፡ ታላላቅ የኢትዮጵያ ፖለቲከኞች ቶሞካ ይመጣሉ፡፡ ቶሞካ ጋዜጣ በጣም ይሸጣል፡፡ ፖሊስ ጋዜጣ የሚነጥቅበት ጊዜም ገጥሞናል፡፡ አሁን የተባረረ አንድ ፖሊስ ነጥቆኝ ያለቀስኩበት ጊዜ ትዝ ይለኛል፡፡
በአራት ሰዓት ከ400 በላይ ጋዜጣ ሸጫለሁ ብለሃል፡፡ አልተጋነነም?
የተጋነነ አይደለም፡፡ በወቅቱ ሸጬአለሁ፡፡ ያኔ ብዙ አዟሪ አልነበረም፡፡ አሁን ሃምሳ ስልሳ አዟሪ ሊኖር ይችላል፡፡ አዟሪ ብዙ ቢሆን እኮ መቼም አንጨርስም፤ በዛ ላይ አምስት ስድስት አይነት ጋዜጦች በቀን ይወጣሉ፤ ከያንዳንዱ አርባ ሃምሳ ጋዜጣ ወስደን እንሸጥ ነበር፡፡ እንግዳው የተባለው አዟሪ ከኔ የበለጠ ጐበዝ ስለነበር በቀን ሰባት መቶ ጋዜጣ ሁሉ ሸጧል፡፡ ከአንድ ጋዜጣ ያኔ ትርፋችን 15 ሳንቲም እኮ ነው፡፡ አሁንም ድረስ “አዲስ ዘመን”ን በየመስርያ ቤቱ ለደንበኞች እሰጣለሁ፡፡
በጋዜጣ ማዞር ሥራህ ምን አተረፍክ?
አንባቢ ያደረገኝ ጋዜጣ መሸጤ ነው፡፡ ጋዜጣ አዟሪ ሁሉ የተቃዋሚ ደጋፊ የሚመስላቸው አሉ፡፡ እኔ ግን ጋዜጣ ማንበብ በጣም እወዳለሁ፡፡ በጋዜጣ አዟሪነቴ አንባቢ ሆኛለሁ፡፡ ማንበብ ስለሚወዱ ብቻ ጋዜጣ እያዞሩ ጋዜጠኛ ሆነው የተቀጠሩ የማውቃቸው ልጆች አሉ፡፡
በቀን 400 ጋዜጣ በምትሸጥ ጊዜ ስንት ብር ታገኝ ነበር?
120 ብር ያህል አገኛለሁ፡፡ ቀይወጥ ያኔ በሦስት ወይ በአራት ብር እንበላለን፡፡ በ1997 ዓ.ም በሸጥኩት ጋዜጣ ብቻ ቤት ገዝቻለሁ፡፡ ያኔ ሳር ቅጠሉ ጋዜጣ ይሸጥ ነበር፡፡ ስራው ብዙ ታዋቂ ሰዎች እና አሳታሚዎችም አስተዋውቆኛል፡፡
አዲስ ጋዜጣ እንዴት ነበር የምታለማምዱት?
ዋናው አርእስት ነው፡፡ የካርቱን ሥዕሎችም ድርሻ አላቸው፡፡ ርዕሱ የጮኸ ጋዜጣ በጣም ይሸጥ ነበር፡፡ እነ “ጦቢያ” በነበሩበት ጊዜ ጋዜጣ በጣም የሚሸጠው ሐሙስ ሐሙስ ነበር፡፡ አዲስ ጋዜጣ አርእስቱ ጐላ ብሎ ይውጣ እንጂ በጣም ነበር የሚሸጠው፡፡ ጋዜጣን የሚያሸጠው ርእስ እንጂ የጋዜጣው አዲስነት ወይም መቆየት አይደለም፡፡
ጋዜጣ አዟሪነቱን ለምንድነው የተውከው?
የሆነ ሰዓት ላይ አላዋጣኝም፡፡ አዟሪም በዛ። አንዳንዶቹ ጋዜጦችም ከህትመት ራቁ፡፡ ጊዜው የፍቅር መፅሔቶች ሆነ፡፡ መፅሔቱንም ሞክሬአለሁ ግን የሚበልጥብኝ ሥራ ሳገኝ ወደዚያ ዞርኩኝ፡፡
የኢንተርኔት መስፋፋት ለጋዜጣ ፈተና ሆኗል ብለህ ታስባለህ?
በጣም የሚገርመኝ ኢንተርኔት ላይ ያነበብነውን መፅሔት ላይ እናየዋለን፡፡ እንደ በፊቱ መረጃ ፈልፍሎ የሚሰራ ብዙ ጋዜጠኛ የለም፡፡ ቢሮ ቁጭ ብሎ ኢንተርኔቱን እየበረበረ ይፅፋል፡፡ እንደበፊቱ ሄዶ የችግሩን ስፋት አይቶ አይደለም የሚፅፈው። ዘመኑ ኢንተርኔት በመፅሔት እየሆነ መጣ፡፡ የኢንተርኔት መኖር በራሱ ችግር የለውም። ሕዝቡ የሚፈልገውን አለማወቅ እንጂ፡፡ አስበው… ጋዜጣ እየቀነሰ መፅሔት እየበዛ ነው፡፡ በዚህ መልኩ መፅሔት ለመስራት ቀላል ነው፤ ኮምፒዩተር ገዝተህ ብሮድባንድ ማስገጠም ነው፡፡
የጋዜጣ ደንበኞችህን እንዴት ነበር የምትይዘው?
ጧት በየቤታቸውና ቢሮአቸው እየወሰድኩ አድዬ፣ ከሰዓት ሂሳቡን ሰብስቤ ወደ ሊስትሮዬ እሄዳለሁ፡፡ አብዛኞቹ ሲከፍሉ መልሱን ያዘው ይሉኛል፡፡ ከዚያ ስመለስ ሲዲ አዞራለሁ፡፡ ቶሞካ ጋዜጣ ጧት እንደወጣ መግባት አለበት፡፡ አንድ ሰዓት ላይ ከሄድክ አይቀበሉህም፡፡ ማለዳ 12 ሰዓት ላይ ከወሰድኩ ግን ቁርስ ሁሉ ይገዛልኛል። ውባየሁና ባለቤቷ አቶ ዘውዱ ናቸው ባለቤቶቹ። ቢሮ ሳይገቡ በጠዋት በበር ሥር አኖርላቸዋለሁ፡፡ ቢሮ ሲከፍቱ ያገኙታል፡፡ ከዚያ በኋላ ዞሬ ሂሳቤን መሰብሰብ ነው።
ፊልም ማሳተምና ማከፋፈል የጀመርከው እንዴት ነው?
ፒያሳ ካሪቢያን በረንዳ ላይ እሰራ ነበር፡፡ አንድ የማውቀው ሰው ከውጭ አምጥቶልኝ የውጭ ሀገር ዘፈን ሲዲ ማዞር ጀመርኩ፡፡ በዚያው የአማርኛ ፊልም ጥያቄዎች በረከቱና እነሱንም ማዞር ያዝኩ። ጐጃም ሙዚቃ ቤት እየሄድኩ ተመላልሼ አወጣ ነበር፡፡ የሙዚቃ ቤቱ ባለቤት ንፁህ አስቻለው እና ወንድሟ ገበያው አስቻለው ቅን ናቸው፡፡ እሷና ወንድሟ “እንዳንተ ካሴት የሚያዞሩት እኮ ፊልም እያሳተሙ ነው፤ ለምን አትሞክረውም፤ እኔ አከፋፍልልሀለሁ” አለችኝ፡፡
ለመጀመርያ ጊዜ ከደቡብ “ካያሞ” የሚል ቪሲዲ አውጥቼ ክልል ድረስ ሄጄ ሸጥኩኝ፡፡ አተረፈኝ። ከዚያ ከመቸርቸር ወደ ማሳተም ተሸጋገርኩ። በመቀጠል “ወይ አዲስ አበባ” የሚል ፊልም ገዛሁ። እንዲህ እንዲያ እያልኩ አሁን ፊልም በስፋት ማሳተም ጀምሬአለሁ፡፡
የትምህርት ደረጃህ እንዴት ነው ?
የካቶሊክ ካቴድራል ትምህርት ቤት የጋዜጣ ደንበኛዬ አባ ተክሌ፣ አንድ ቀን ጋዜጣ ሳደርስላቸው “ትማራለህ?” ሲሉ ጠየቁኝ “አልማርም፤ ከሰባተኛ ክፍል ነው ያቋረጥኩት” አልኳቸው፡፡ ከዚያ በካቶሊክ ካቴድራል ትምህርት ቤት በነፃ እንድማር ፈቀዱልኝ፡፡ ትምህርቴን እዚያ ጨርሴ ነው ኤዲቲንግ የተማርኩት፡፡ የሴቶች ፀጉር ሥራም ተምሬአለሁ፡፡ አሁን እንግዲህ አስር ያህል ፊልሞች አሳትሜአለሁ፤ ገና ያልወጡም አሉ፡፡ “ኦ ያበሻ ሴት”፣ “ሌዲስ ፈርስት” “ሀረግ”፣ “ሜድ ኢን ቻይና”፣ “የዜግነት ክብር” እና ሌሎችን አሳትሜአለሁ፡፡
በተለያየ ምክንያት በተለይ በሕገወጥ ቅጂ የከሰሩትን ፊልሞች ጭምር ሃላፊነት ወስደህ አከፋፍለሃል ይባላል፡፡ እንዴት አላከሰረህም?
ስም ያላቸው ስለነበሩ ተሸጠዋል፡፡ ግን ስገባበትም አልፈራሁም፡፡ ሥራውን በጣም ነው የማውቀው፡፡ ፊልሞቹ የተሰረቁም እንኳ ቢሆኑ የመታየት አቅም እንደነበራቸው አውቃለሁ፡፡ እስካሁን ፊልሞች ለመግዛት የከፈልኩት ከፍተኛው 140 ሺህ ብር ሲሆን ዝቅተኛው ዘጠኝ ሺህ ብር ነው፡፡ የቅጂ መብት እንዲከበር የሕዝቡ ግንዛቤ መጨመር አለበት፡፡
በዚህ ረገድ የኦዲዮ ቪዥዋል አሳታሚዎች ማህበር ሃላፊዎች እነ ኃይላይ እና እቁባይ እንዲሁም ሌሎቹም ሊመሰገኑ ይገባል፡፡ አሁን ደግሞ ሕገወጥ ቅጂ በሲዲ መሆኑ ቀርቶ በፍላሽ እና በሚሞሪ ሆኗል። ይኼን ለማስቀረት ብዙ ጥረት ያስፈልጋል፡፡
የሚሸጥና የማይሸጥ አልበም ዘፈኑን ሰምተህ እንድትለይ ያመጡልሃል ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ እውነት ነው?
በነገራችን ላይ ውሎዬ ከታዋቂው ሙዚቀኛ መስፍን ታምሬ ጋር ነው፡፡ እሱ ብዙ ነገር አስተምሮኛል፡፡ ዘፋኞች አስተያየት ለመጠየቅ ወደኔ ይመጣሉ፡፡ ለምሳሌ አንዱን አርቲስት “ፖስተር” አሳምር እንጂ ይሸጥልሃል ብዬው እንዳልኩት ተሸጦለታል፡፡ ሙዚቀኛ አይደለሁም፡፡ በሙዚቃው ቢዝነስ እንደመቆየቴ ግን በደንብ ታሽቻለሁ፡፡ “የትዝታ ትዝታ” ሲወጣ ይኼ ሲዲ ሁለት አመት ይነግሳል ብዬ ነበር፡፡ ሌላው ሲፈራ እኔ በርካታ ኮፒዎች ወስጄ ሸጫለሁ፡፡ ሲዲው አሁንም እየተሸጠ ነው፡፡
ባህልና ቱሪዝም ቢሮ በግምገማ ብቁ አይደሉም ያላቸው ፊልሞች አንዳንዴ በዲቪዲ ይመጣሉ፡፡ እነዚህንስ ገዝተሃል?
በጭራሽ አልገዛም፡፡ መስፈርቴ ፊልሙ በዓለም ሲኒማ መታየቱ እና ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ብቁ ነው ማለቱ ነው … ብቃት የሌላቸው ፊልሞች አልገዛም። ዓለም ሲኒማ ቤት ካልታየ አልገዛም፡፡ ቢኒያም ወርቁ “ሰባተኛ ሰው” የተባለ ፊልሙን እምነት ጥሎብኝ ሸጫለሁ፤ በጣም አከብረዋለሁ፡፡ ይኼው ፊልም ወደ ዲቪዲ ሲመጣ ርእሱንና ፖስተሩን ለውጩ ነው ለገበያ ያበቃሁት፡፡ በጣም ሲሸጥ፣ ገረመኝ፡፡ አሜሪካ ውስጥ ያለ አከፋፋይም በጣም እንደተሸጠለት ነግሮኛል፡፡
የወደፊት እቅድህ ምንድነው?
ከታዋቂ ተዋንያን ጋር በመሆን ፊቸር ፊልም ለመስራት በዝግጅት ላይ ነኝ፡፡ ቀረፃ በቅርቡ ይጀመራል፡፡ “ያንቺው ሌባ” የሚለውን ፊልም ደግሞ ሰሞኑን አወጣለሁ፡፡
በመጨረሻ የምትለው ነገር ካለ---
እዚህ ሥራ እንድገባ ለረዱኝ ለንፁህ፣ ለገበያው፣ ለመስፍን ታምሬና ለአስተማሪው አባ ተክሌ፤ እንዲሁም ቤተሰቦቼንና አዲስ አድማስን አመሰግናለሁ፡፡ እዚህ ስላደረሰኝ ለጋዜጣው ልዩ ትዝታ አለኝ፡፡ የጋዜጣው ባለቤቶች ባያውቁኝም እኔ አውቃቸዋለሁ፡፡

Published in ጥበብ

“...እስከአሁን የማልረሳው አንድ አጋጣሚ አለኝ፡፡ አንዲት እናት በቤትዋ ሳለች ምጥ ጀምሮአታል፡፡ ከዚያም ይበልጥ ስትታመምባቸው እኔ ወዳለሁበት በሲዳማ ዞን ቦና ዙሪያ ወረዳ ባለው የጤና ጣቢያ ያመጡአታል፡፡ እኔም ስመለከታት የማህጸን መተርተር ደርሶባታል፡፡ አጋጥሞኝ ስለማያውቅ እጅግ በጣም ነበር የደነገጥኩት፡፡ በእርግጥ በኦፕራሲዮን ማህጸንዋ ይወጣል። ነገር ግን እሱም እርምጃ ቢወሰድ እና ሕይወቷ ቢተርፍ ማህጸንዋ ሲወጣ ወደፊት ልጅ መውለድ ስለማትችል ባለችበት ሕብረተሰብ አስተሳሰብ የምትገለል ትሆናለች፡፡ ምክንያቱም ልጅ ለወደፊቱ መውለድ ስለማትችል የነበራት ባልም ይፈታታል... ሌላ ባልም አያገባትም፡፡ በህብረተሰቡም ዘንድ ተቀባይነት ስለማይኖራት ዝም ብላ የምትኖር ትሆናለች፡፡ይሄንን ነገር ዛሬ ላይ ሳስበው ይቆጨኛል፡፡ ምክንያቱም እንደአሁኑ እውቀቱ ቢኖረኝ ኖሮ ወደከፍተኛ ሕክምና ጊዜ ሳልፈጅ አስተላልፌ በሴትየዋ ላይ የደረሰው ችግር ሊቃለል ይችል ነበር…”
ከላይ ያነበባችሁት ገጠመኝ ከአንድ የጤና መኮንን የቀረበ ነው፡፡ የጤና መኮንኑን ያገኘነው በሐዋሳ በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር እና በዞኑ የጤና መምሪያ እንዲሁም በፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ትብብር WATCH (women & their child health) የእናቶችና ሕጻናት ጤናን ለማሻሻል በተነደፈው ፕሮጀክት ድጋፍ ስልጠና ሲወስድ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር WATCH (women & their child health) የተሰኘው ፕሮጀክት አስተባባሪ የሆኑት አቶ ቢንያም ጌታቸው እንደሚገልጹት ድጋፍ የሚገኘው ከካናዳ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ሲሆን በዋናነት የሚሰራውም የእናቶችን እና ሕጻናትን ሞት መቀነስ ነው፡፡ ስለዚህም ከዚህ ማህበር ጋር በመተባበር የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር Basic emergency obstetric & new born care (መሰረታዊ የሆነ አጣዳፊ የእናቶችና የህጸናትን ሞት መቀነስ) የሚባለውን የስራ እንቅስቃሴ ስልጠና እና ለጤና ጣቢያዎች የአቅም ድጋፍ የማድረግ ስራ እየሰራ ይገኛል፡፡ የWATCH ፕሮጀክት በኢትዮጵያ ውስጥ በሶስት ክልል ውስጥ በሚገኙ 8/ ስምንት ወረዳዎች ተግባሩን እያከናወነ ሲሆን ይኼውም በደቡብ ሲዳማ ዞን፣ በኦሮሚያ ጅማ ዞን፣ በአማራ ክልል በሰሜን ወሎ ዞን ነው፡፡
በካናዳ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አማካኝነት በተዘረጋው በዚህ ፕሮጀክት ከውጭ በመጡ ባለሙያዎች የኢትዮያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አባል ለሆኑ ከፍተኛ ሐኪሞች ስልጠና ተሰጥቶ የነበረ ሲሆን እነዚህ የሰለጠኑ ባለሙያዎችም ከተለያዩ ወረዳዎች ለመጡ የጤና ባለሙያዎች መሰረታዊ የሆነ አጣዳፊ የእናቶችና የህጸናትን ሞት በመቀነስ ረገድ ክህሎትን እያስጨበጡ ይገኛሉ ብለዋል የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አቶ ቢንያም ጌታቸው፡፡
በማሰልጠን ተግባር ላይ ከተሰማሩት የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትና በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት ዶ/ር ይፍሩ ብርሀን እንደሚሉት ለእናቶች ሞት ምንክያት የሚሆኑት ነገሮች በሶስት ወይንም በአራት ሊከፈሉ ይችላሉ፡፡
1/ እናቶችና ቤተሰቦቻቸው የጤና አገልግሎት ለማግኘት አለመፈለግ፣
እነዚህ እናቶች የጤና ችግር ሲያጋጥማቸው በአካባቢው አዋላጅ ነርሶች አማካኝነት ለመውለድ መዘጋጀት ወይንም ምንም ክትትል አለማድረግ እንዲሁም የጤና ችግር ሲገጥማቸው በአፋጣኝ ወደ ጤና ተቋም ወይንም ሆስፒታል አለመምጣት ነው፡፡
2/ በሚኖሩበት አካባቢ የህክምና አገልግሎት የሚሰጥ ተቋም አለመኖር ፣
3/ ወደጤና ተቋም ከመጡ በሁዋላ የጤና ባለሙያው የደረሰባቸውን ችግር ለይቶ አለማወቅ፣...ይህ በአሁኑ ወቅት እንደከፍተኛ ችግር የሚቆጠር ነው፡፡ ምክንያቱም ይህ የሚያሳየው የእውቀት ችግር መኖሩን ሲሆን በዚህም ምክንያት ለእናቶቹ በጊዜው አስፈላጊው ሕክምና የማይሰጥ እና ወደከፍተኛ ሕክምና እንዲተላለፉ አለመደረጉን ነው፡፡ አንዳዶች ሕመም ሲጠናባቸው ወደአቅራቢያው ጤና ተቋም ሲሄዱ በዚያ በሚፈጠረው አላስፈላጊ መዘግየት ምክንያት ሕይወታቸው ከአደጋ ላይ ይወድቃል፡፡ አልፎ አልፎም አግባብ ያልሆነ ሕክምና የሚሰጥበት አጋጣሚ ስለሚኖር ይህንን ክፍተት የሚሞላ አሰራር መኖር አለበት፡፡ ስለዚህም እስከአሁን ባየነው የስልጠና ሂደት ሰልጣኞቹ ሲመጡ የነበራቸው የእውቀት ደረጃ እና ሲጨርሱ የሚኖራቸው ደረጃ በጣም ይለያያል ብለዋል ዶ/ር ይፍሩ ብርሀን፡፡
ሌላው አሰልጣኝ ዶ/ር እንዳለ ሲሳይ ይባላሉ፡፡ ዶ/ር እንዳለ በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ የማህ ጸንና ጽንስ ሐኪምና አስተማሪ ናቸው።
“...ይህ ሆስፒታል ሪፈራል ሆስፒታል ስለሆነ ከሌሎች የህክምና ተቋማት የተላኩ ታካሚ እናቶችን ያስተናግዳል፡፡ ነገር ግን በአብዛኛው የሚመጡ እናቶችን ለማዳን በጣም ፈታኝ የሚሆን ሲሆን ይህም ወደሆስፒታሉ የሚልኩ የጤና ተቋማት ጊዜን በአግ ባቡ አለመ ጠቀማቸው ነው፡፡ ለባለሙያዎቹ ስልጠና የሚሰጠው በሚሰሩበት ጤና ተቋማት ባላቸው አቅም ሊያክሙ የሚችሉትን እንዲያክሙና ከአቅማቸው በላይ የሆነውን ግን ጊዜ ሳይ ፈጁ ወደከፍተኛ ሕክምና እንዲልኩ የሚያስችል ነው። ምን አይነቱ የጤና ችግር በጤና ጣቢያ ሊታከም ይችላል? የሚለውን የመለየትና አቅምን የማወቅ ክህሎት አብሮ በስል ጠናው ይሰጣል፡፡ በእርግጥ ስልጠናው አዲስ እውቀትን ከመስጠት የሚጀምር ሳይሆን የነበራቸውን እውቀት እንዴት በስራ ላይ እንደሚያውሉት አቅጣጫ የሚያሳይ ነው፡፡ ነገር ግን ሰልጣኞች አንዳንድ ጊዜ በሚሰጣቸው የልምምድ ተግባር አድናቆት ሲያሳዩ ይታያሉ፡፡ ምክንያቱም በተግባር እንዴት እንደሚፈጽሙት አያውቁምና ነው፡፡ አንዲት እናት እነርሱ ወዳሉበት ጤና ተቋም ስትመጣ በምን መንገድ እንደሚረዱዋት ወይንም በፍጥነት ወደከፍተኛ ህክምና ተቋም እንደሚልኩዋት ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ያለውን አሰራር በሚያዩበት ጊዜ እንደ አዲስ ትምህርቱን ሲቀበሉ ይታ ያሉ፡፡ ይህ ማለት ቀደም ብሎ የነበራቸው ልምድ ምን ያህል እንደነበርና አሁን ምን ያህል እውቀት እንዳገኙ የሚያሳይ ስለሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ክፍተት እንደነበረ የሚያ ረጋግጥ ነው፡፡ ልምምድ የሚያደርጉት በሞዴልነት በተሰሩ የሰውነት ክፍሎች ሲሆን ወደሰው ከመቅረባቸው በፊት ተገቢውን ያህል ስራ እንዲሰሩ ይደረጋል። ከዚያም ወደሆ ስፒታሉ በመግባት ከባለሙያዎች ጋር በመሆን ሰዎችን እንዲረዱ ይደረጋል፡፡ በዚ ህም ከቀን ወደቀን የመስራት ፍላጎትና ብቃታቸው እያደገ ሲሄድ ይስተዋላል፡፡ ስለ ዚህ ስል ጠናው የብዙ እናቶችና ሕጻናት ሕይወት እንዲተርፍ ያስችላል የሚል እምነት አለ ብለዋል ዶ/ር እንዳለ ሲሳይ፡፡
ከሲዳማ ዞን ሸበዲኖ ወረዳ የመጣ ክሊኒካል ነርስ ቀደም ሲል በስራው አለም የገጠ መውን ሲያስታውስ፡-
“...እኔ በምሰራበት ጤና ተቋም አንዲት እርጉዝ ሴት ከእግር እስከራስዋ እየተንቀጠቀጠች እራስዋን ስታ በሰዎች ሸክም ትመጣለች፡፡ እርግዝናው ቀኑን የገፋ ነው፡፡ አብረዋት የመጡ ቤተሰቦችዋ እርስ በእርስ አልተስማሙም፡፡ ገሚሱ የቤት ጣጣ ነው ይላል፡፡ ገሚሱ ደግሞ ለጸበሉ ይደረስበታል መጀመሪያ ሐኪም ይያት ይላል፡፡ እኔ ግን እንደዚያ አይነት ነገር አይቼ ስለማላውቅ ግራ ገባኝ፡፡ ነገር ግን ለማንኛውም ብዬ... ግፊትዋን ስለካ ደምዋ በጣም ከፍ ብሎአል፡፡ በጊዜው ለእሱ የሚሆን መድሀኒትም አልነ በረኝም፡፡ ጊዜ ወስጄ...ያለውን ነገር ፈላልጌ እንደምንም ሰጥቼ በስተመጨረሻው እጄ ላይ ሳትሞትብኝ ወደሆስፒታል ይዘው እንዲሄዱ አደረግሁኝ፡፡ ነገር ግን ሆስፒታል ስትደርስ ሁኔታው እጅግ አስቸጋሪ እንደነበር አውቄአለሁ፡፡ አሁን እንደተማርኩት ቢሆን ኖሮ ...ሁኔታው ከእኔ አቅም በላይ ስለሆነ ምንም ጊዜ ሳልፈጅ በአስቸኳይ ወደከፍተኛ ሕክምና እልካት ነበር፡፡ ወደፊት ግን በሰለጠንኩት መሰረት የምችለውን ሕክምና እሰጣለሁ...እኔ የማልችለውን ግን አላስፈላጊ መዘግየትን አስወግጄ ቶሎ ወደ ከፍተኛ ሕክምና እልካለሁ...” ብሎአል፡፡
ደቡበ ሲዳማ ዞን ሐዋሳ ውስጥ ስልጠና ሲወስዱ ከነበሩት መካከል አቶ ሳምሶን ሰንበቶ ከቦና ዙሪያ ወረዳ እንደገለጸው የእናቶችን ጤንነት በተመለከተ በሐዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል እየ ሰለጠኑም ተግባሩንም ከቀደምት ሐኪሞች ጋር በመሆን በመስራት ተገቢውን ልምምድ እያደረጉ ነው፡፡ በተለይም የእናቶችንና የህጸናትን ጤንነት በተመለከተ የተሰጠው ስልጠና መሰረታዊና ህብረተሰቡንም ለማገልገል የሚያስችል ነው እንደ አቶ ሳምሶን ሰንበቶ አስተያየት፡፡ እኔ ባለሁበት አካባቢ እናቶችም ሆኑ ጨቅላ ሕጻናቶች ብዙውን ጊዜ የሚሞቱት ከወሊድ ጋር በተያያዘ ሲሆን በዚህ ምክንያት የሚፈጠረውን ክፍተት ለመዝጋት ሙሉ በሙሉ ባይሆንም በተቻለ መጠን የሚያግዝ እውቀትን ጨብጠናል ብዬ አምናለሁ ብሎአል አቶ ሳምሶን ሰንበቶ፡፡
የWATCH ፕሮጀክትን ተግባራዊ በማድረግ ረገድ ከESOG ጋር በትብብር የሚሰራው የፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ የደቡብ ማስተባበሪያ ጽ/ቤት የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ገዳምነሽ ደስታ ትባላለች፡፡ ፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ከፕላን ካናዳ እና ከሲዳ ያገኘውን ብር Berehan integrated community development organization በመስጠት ይህ ፕሮጀክት በተያዘለት አላማ መሰረት በሲዳማ ዞን በሶስት ወረዳ ላይ በትክክል በመሰራት ላይ መሆኑን ይቆጣጠራል፡፡ የኢትዮያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበርም ቴክኒካል አማካሪ በመሆን በሶስቱ ወረዳዎች ለሚገኙ እና በዞኑ የጤና መምሪያ ክትትል ምርጫው ተካሂዶ ሰልጣኞች ሲላኩ የስልጠናውን ሂደት በማከናወን የድርሻውን ይወጣል፡፡ በተጨማሪም ሰልጣኞቹ ወደሚሰሩበት ጤና ጣቢያ በሚመለሱበት ጊዜ ስራ ላይ የሚያውሉትን የህክምና መገልገያ መሳሪያና መድሀኒትን ግዢ በሚመለከትም ESOG ያማክራል፡፡ ስለዚህም ፕሮጀክቱ በአሁኑ ወቅት የሚሰራው ሁለት ነገር ላይ ሲሆን አንደኛው አቅም ማጎልበት እንዲሁም ሌላው ደግሞ በመንግስት ተዘርግቶ ባለው የጤና ስርአት ውስጥ ያሉ ክፍተቶችን ማሟላት ነው። ስለዚህም እናቶችና ሕጻናት የሚገጥ ማቸውን የጤና ችግር ለማቃለል በትብብር መሰረታዊ ስራ እየተሰራ ያለበት ደረጃ ላይ ነን ብለዋል ከፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ገዳምነሽ ደስታ፡፡
ይቀጥላል

Published in ላንተና ላንቺ

የዛሬ አምስት ወር ገደማ ከአውሮፓና ከመካከለኛው ምስራቅ ተጠራርተው፣ በኳታሯ መዲና ከአንዱ የስብሰባ አዳራሽ ወደ ሌላኛው ሽር ብትን ሲሉ የነበሩትን የሶርያ ተቃዋሚዎች “የወቅቱ ዋነኛ አጀንዳችሁ ምንድን ነው?” ብላችሁ ብትጠይቋቸው፣ ሁሉም በአንድ ቃል የሚሰጧችሁ መልስ ከቀናት ምናልባት ግፋ ቢልም ከሳምንታት በኋላ ስለሚያቋቁሙት አዲሱ የሶርያ መንግስትና ስለሚመሠርቷት አዲሷ ሶርያ ብቻ ነበር፡፡
ከዛሬ ሁለት አመት በፊት በቱኒዚያ የተቀጣጠለውን የአረብ ህዝባዊ አብዮት ተከትሎ በተቀሰቀሰው ህዝባዊ አመጽ፣ የፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድን መንግስት ለመጣል ነፍጥ አንግበው ግብግብ የገጠሙት አማጽያን፣ በወቅቱ በጦር ሜዳው ጐራ እያደረጉት የነበረውን ትግልና ግስጋሴ በቅጡ ከተገነዘባችሁ፣ የተቃዋሚዎችን ይህን መሰል መልስ ለመጠራጠርና ምናልባትም የቀጣዩን ቀን ብርሃን ለማየት የማይበቃ ዋጋ ቢስ ቀቢፀ - ተስፋ ነው በሚል ለመሟገት አትዳዱም፡፡
እርግጥ ነው በዚያን ወቅት የመንግስት ወታደሮች እግራቸው በረገጠው ቦታ ሁሉ፣ የተቃዋሚዎችና የደጋፊዎቻቸው ይዞታ ነው የተባለውን አካባቢ ሁሉ ባገኙት መሳሪያ በምድርና በአየር እየደበደቡ፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ሶርያውያንን መፍጀታቸውን ለአፍታም ቢሆን አላቆሙም ነበር፡፡
ይሁን እንጂ በዚያን ወቅት ለወትሮው ተከፋፍለው እርስበርስ በመናቆር የሚታወቁት የሶርያ ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ አንድ አላማና አቋም የያዙ መስለው ታይተው ነበር፡፡ ያ ወቅት የበሽር አልአሳድ መንግስት ጉድጓዱ የተማሰ፣ ልጡ የተራሰ እንደሆነ በብዙዎች ዘንድ ተገምቶ ነበር፡፡ ይህንን የብዙዎች ግምት በዋናነት መሰረት ያደረጉ ግንባር ቀደም አለምአቀፉ የዜና አውታሮች፣ የጧትና ማታ የዜና እወጃቸው፣ የመንግስት ወታደሮች ቅጥ የለሽ የጅምላ ድብደባ፣ የጣር ድብደባ እንደሆነና የፕሬዚዳንት በሽር አልአሳድ ጉዳይ ያለቀ የደቀቀ መሆኑን የሚያስረዳ ነበር፡፡
ይህንን ትንታኔ መሠረት ያደረጉና በተቃዋሚዎች የሚመሠረተውን አዲሱን የሶርያ መንግስትና አዲሲቷን የድህረ አሳድ ሶርያን በራስ አምሳያ ለመፍጠር ያለሙ ሁሉ፣ የመንግስት ወታደሮች ድብደባ እያደረሰ ያለውን ሰብአዊ ቀውስ ለማስቆም በሚል ሰበብ፣ ቀጥተኛ ሁሉን አቀፍ ጣልቃ ገብነት ለመፈፀም ቋምጠው ነበር - ከቻይናና ከራሺያ በስተቀር፡፡
ከመካከለኛው ምስራቅ አንስቶ እስከ አሜሪካና አውሮፓ ድረስ ሶርያን በተመለከተ ዋነኛ የውይይት አጀንዳ የነበረው አዲሲቷን ሶርያ ለመፍጠርና ለማቋቋም እንዴት ቻይናና ራሺያን ማግባባት ይቻላል የሚለው ጉዳይ ነበር፡፡ የሶርያ ህዝባዊ አመጽ ከተቀጣጠለበት ከዛሬ ሶስት አመት ጀምሮ ቻይናም ሆነች የፕሬዚዳንት ፑቲኗ ራሺያ አቋማቸውን በግልጽ ከማስረዳት ፈጽሞ ቦዝነው አያውቁም፡፡ ትናንትም ሆነ ዛሬ የፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድን መንግስት በሀይል ለመገልበጥ የሚደረግን ማናቸውንም አይነት የውጭ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት የምራቸውን እንደሚቃወሙ ሁልጊዜ በይፋ እንደገለፁ ነው፡፡
አሜሪካና የአውሮፓ ወዳጆቿም፤ ቻይናና ራሺያ የያዙትን አቋም ቀይረው ፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድን ለማስወገድ ከጐናቸው እንዲቆሙ ለማድረግ፣ በእርስ በርስ ጦርነቱ የተነሳ በተለይም በመንግስት ወታደሮች የጅምላ ድብደባ አማካኝነት በሶርያ የደረሰውን አስከፊ ሰብአዊ ቀውስ እንደዋና ምክንያትነት በመጠቀም የቻሉትን ያህል ለማሳመን ጥረው ነበር፡፡ እንደእውነቱ ከሆነም ነገርዬው ከአለም አቀፉ የብሔራዊ ጥቅምና የዲፕሎማሲ ቁርቁስ በላይ ነበር፡፡
ከዛሬ አምስት ወር በፊት የተባበሩት መንግስታት ያወጣው መረጃ፣ የእርስ በርስ ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ከአንድ መቶ ሺ የሚልቁ ሶርያውን ህይወታቸውን እንዳጡና አንድ ነጥብ ዘጠኝ ሚሊዮን የሚሆኑት ደግሞ ቤት ንብረታቸውንና ቀያቸውን ጥለው ወደ ጐረቤት ሀገራት እንደተሰደዱ ያስረዳል፡፡
የሊቢያውን አምባገነን መሪ ኮሎኔል ሙአመር ጋዳፊን ከስልጣናቸው ለማስወገድ በተወሰደው የኔቶ ወታደራዊ እርምጃ፤ በአሜሪካና በአውሮፓ አጋሮቿ “አይሆኑ አሸዋወድ ተሸውደን ተጃጅለናል” ያሉት ቻይናና ራሺያ ግን በዚህ የሶርያ ሰብአዊ ቀውስና በቀረበላቸው የእልቂትና የሰቆቃ መረጃ ለአፍታም ቢሆን ልባቸው ሊራራ አልቻለም፡፡ ዛሬም የያዙት አቋም አንድ ነው፡፡ ልክ እንደ ትናንቱ ሁሉ ዛሬም የውጪ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነትንና በሶርያ ላይ የሚወሰድን ወታደራዊ እርምጃ አጥብቀው እንደሚቃወሙ ግልጽ አድርገዋል፡፡
ዛሬ በሶርያ ያለው ጠቅላላ ሁኔታ የዛሬ አምስት ወር ከነበረው በእጅጉ የተለየ ነው፡፡ እናም አሁን የሶርያን ተቃዋሚዎች “ነገሩ እንዴት ነው” ብትሏቸው፣ ጨርሰው ባላሰቡትና ይሆናል ብለው ባልገመቱት ሁኔታ በሼህ ናስሩላህ የሚመራው የሊባኖስ የሂዝቦላ ተዋጊዎች የፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድን መንግስት በመደገፍ የውጊያውን አውድማ በመቀላቀላቸው፣ ሊጨብጡት በእጅጉ ተቃርበው የነበረውን የረጅም ዘመን ህልማቸውን እንዳጨናገፉባቸው ይነግሯችኋል፡፡
ይህ ደግሞ አንዳችም ሀሰት ነገር የለውም። ትናንት አለቀላቸው የተባሉት ፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድ፤ ድል እየቀናቸው ተቃዋሚ አማፂያንን ይዘውት ከነበረው አካባቢ እያስለቀቋቸው ይገኛሉ። እየወሰዱት ያለው የጭካኔ እርምጃም ግለቱን አልቀነሰም፡፡
ሶቪየት ህብረትን ከሠላሳ አመታት በላይ ሰጥ ለጥ አድርጐ የገዛው ጓድ ዋና ፀሐፊ ጆሴፍ ስታሊን፤ በአንድ ወቅት የሰዎችን መንጋ እልቂት አስመልክቶ “የአምስትና አስር ሰው ሞት አሳዛኝ ነገር ነው። የሺዎች እልቂት ግን ተራ ስታቲስቲክስ ነው፡፡ በማለት እንደተናገረ በተደጋጋሚ ይነገራል፡፡ የፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድ ነገርም እንዲሁ ነው፡፡ ለእሳቸው የመቶ ሺ ሶርያውያን ወገኖቻቸው እልቂት አሳዛኝ ክስተት ሳይሆን ተራ የስታቲስቲክስ ጉዳይ ነው፡፡ ፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድ የአባታቸው ልጅ ናቸው፡፡ በ1971 ዓ.ም የፖለቲካ የጡት አባታቸው የነበሩትን ጀነራል ሳላህ አልጀዲድን በወታደራዊ ሃይል ገልብጠው ስልጣን ላይ በመውጣት፣ በከባድ የልብ ህመም የተነሳ ህይወታቸው እስካለፈበት እስከ 2000 ዓ.ም ድረስ ለሃያ ዘጠኝ አመታት ድፍን ሶርያን ከብረት በጠነከረ እጃቸው አንቀጥቅጠው መግዛት ብቻ ሳይሆን ዘመናዊ የአሳድ ፕሬዚዳንታዊ ስርወ መንግስት መመስረት የቻሉት አባታቸው ፕሬዚዳንት ሀፌዝ አል አሳድ፤ በተግባር እያሳዩ ያሳደጓቸው የሶርያውያን ህይወት ከእርሳቸው ስልጣን የበለጠ ዋጋ እንደማያወጣ ነው፡፡
የአይን ህክምና የዶክትሬት ትምህርታቸውን ለመከታተል ወደ አውሮፓ ከመሄዳቸው በፊትም በ1982 ዓ.ም በሙስሊም ወንድማማቾች ድርጅት አማካኝነት የተነሳባቸውን ጠንካራ ተቃውሞ፣ ከሃያ ሺ በላይ የሆኑ የሙስሊም ወንድማማቾች ድርጅት መሪዎችን፣ አባላትንና ደጋፊዎችን በሃማ ከተማ ልዩ የደህንነት ኮማንዶ ጦራቸውን በማሰማራት ያለ ርህራሄ በማስጨፍጨፋቸው የተነሳባቸውን ተቃውሞና አመጽ ፀጥ ረጭ ሲያደርጉ፣ ወጣቱ ባሻር አልአሳድ በአይናቸው በብረቱ አይተዋል። ከዚያን ጊዜ በኋላም ፕሬዚዳንት ሃፌዝ አልአሳድ ለተቃዋሚዎቻቸው እንዴት ያለ ጠንካራ ክንድና ድርብ አንጀት እንደነበራቸው ህይወታቸው እስካለፈበት ጊዜ ድረስ በሚገባ ተገንዝበዋል፡፡
እና ታዲያ የማን ዘር ጐመን ዘር! በአባታቸው እግር የተተኩት ፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድም፣ በአመጽ ለተነሱባቸው ተቃዋሚዎቻቸው የሚዝል ክንድም ሆነ የሚራራ አንጀት ጨርሶ አልነበራቸውም፡፡ ከእርሳቸው ስልጣን የሚበልጥ ምንም ነገር የለምና እንኳን በመቶ ሺዎች ቀርቶ በሚሊዮኖችም ቢሆን የሶርያውን ህይወት ቢጠፋ ከቁም ነገር የሚጥፉት ጉዳይ አይደለም፡፡
የአማፂያኑን አከርካሪና የደጋፊዎቻቸውን ቅስም ለመስበር፣ በአየርና በምድር ያልተጠቀሙት የመሳሪያ አይነት አልነበረም፡፡ ሰሞኑን ግን ከአጋሮቻቸው ቻይናና ራሺያ በስተቀር ድፍን አለም የፈራው ደርሷል፡፡ በሺ የሚቆጠሩ ሶርያውያን በኬሚካል የጦር መሳሪያ ጥቃት ያለ ርህራሄ ተጨፍጭፈዋል፡፡
ፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድ፤ “ጭፍጨፋውን ሆን ብለው ያደረሱት የአማጽያኑ ወታደሮች እንጂ እኔስ የኬሚካል ጦር መሳሪያ በዞረበትም አልዞርኩ” በማለት ማስተባበያቸውን ሰጥተዋል። የሚያምናቸው ግን ጨርሶ ማግኘት አልቻሉም፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ለአስራ ሶስት አመታት በዘለቀው የስልጣን ዘመናቸው በተቃዋሚዎቻቸው ላይ ሲፈጽሙት የነበረውን አስከፊ ድርጊት ይቅር ቢባሉ እንኳ አመጽ ከተቀሰቀሰበት ጊዜ ጀምሮ ሲሰነዝሩት በነበረው እጅግ አሰቃቂ ጥቃት የተነሳ ሰውየው ያሉትን አምኖ ለመቀበል ያዳግታል፡፡ ቀድሞ ነገር ሰውዬው እኮ የአባታቸው ልጅ ናቸው!
የአሁኑ የኬሚካል ጦር መሳሪያ ጥቃት ግን እንዳለፉት ጊዜያት ጥቃቶች በቸልታ የሚታለፍ አልሆነም፡፡ ምንም እንኳ ፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድ አልፈፀምኩም ብለው ምለው ቢገዙቱም፣ አሜሪካና የአውሮፓ አጋሮቿ ከእርሳቸው ራስ አንወርድም ብለዋል፡፡
አሜሪካ በተለይ በዚህ ብቻ አልተወሰነችም። “የፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድን ወታደሮች ደምስሼ የስልጣን ገመዱን ባላሳጥረው አገር ብላችሁ አትቁጠሩኝ” ብላ አካኪ ዘራፍ ፎክራለች፡፡ የመከላከያ ሚኒስትሯ ቸክ ሀግልም “አስፈላጊውን ወታደራዊ ዝግጅት አጠናቀን እየጠበቅን ያለነው፣ የፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማን ተኩሱ የሚል ትዕዛዝ ብቻ ነው” በማለት የአሜሪካ ፉከራ ተራ ፉከራ እንዳልሆነ በግልጽ አሳውቀዋል፡፡ ራሺያም በበኩሏ እስኪ የምታደርጉትን አያለሁ ብላለች። መንግስታዊው “ኮስሞፖልስኪ ፕራቭዳ” የተሰኘው ጋዜጣ፤ “ራሺያ እንደሌላው ጊዜ እጇን አጣጥፋ በማስጠንቀቂያ ብቻ ትቀመጣለች ብሎ የሚገምት ካለ እርሱ እርሙን ያውጣ” በማለት አስፈራርቷል፡፡
አሁን ባለው አጠቃላይ የሶርያ ሁኔታ ሁለት ነገሮች እርግጠኛ የሆኑ ይመስላል፡፡ አንደኛው አሜሪካ ተባባሪ አገኘች አላገኘች ወታደራዊ እርምጃ መውሰዷና ፕሬዚዳንት በሻር አልአሳድ ከስልጣናቸው መፈናቀላቸው ነው፡፡ ቁርጡ ያልታወቀውና መጨረሻውን ለማወቅ የሚያጓጓው ደግሞ ራሽያ የዛተችውን ታደርግ ይሆን? ወይስ “ቆይ ነገ አገኝሻለሁ” ብላ በዛቻ ብቻ ትቀራለች? የሚለው ጉዳይ ነው፡፡ ጊዜ ለዚህና ለሌሎችም ተያያዥ ጉዳዮች ምላሹን ይሰጠናል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

“በርናባስ” በ2005 ዓ.ም ማጠናቀቂያ ላይ ለአንባቢያን የቀረበ ረጅም ልቦለድ ታሪክ ነው፡፡ በደራሲ ትዕግሥቱ ተክለማርያም የተዘጋጀው መጽሐፉ፤ በ353 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን በኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር እና በብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት የህትመት ተዟዟሪ ፈንድ የታተመ ነው፡፡
ጽናት፤ የመጽሐፉ ማዕከላዊ መልዕክትና ጭብጥ ነው፡፡ ከዋና ገፀ ባሕሪያት የአንዱ ሥም ነው የመጽሐፉ ርዕስ የሆነው፡፡ “የመጽናት ልጅ” የሚል ትርጉም ያለው ይሄ ስያሜ፤ ከመጽሐፍ ቅዱስ የተወሰደ ነው፡፡ እምነቱ፣ ጽናቱና ታማኝነቱ ተረጋግጦለት “የመጽናት ልጅ” የተባለው የመጽሐፍ ቅዱሱ በርናባስ፤ የእርሻ መሬቱን የሸጠበትን ገንዘብ በሙሉ ለሐዋርያት ወስዶ በመስጠቱ ምክንያት ነበር ዮሴፍ የሚለው ቀዳሚ መጠሪያው ተቀይሮ በርናባስ የተባለው፡፡
“በርናባስ” የረጅም ልቦለድ ታሪክም ተመሳሳይ መልዕክት የያዘ ነው፡፡ ጽኑ ሆኖ ያሰቡት ግብ ላይ ለመድረስ ግን የሚታለፈው ችግርና መከራ ጥልቅና ሰፊ መሆኑን ብቻ ሳይሆን፤ ጽናት ምንድነው? መጽናትና አለመጽናትስ በምን ይመዘናል? መጽናት ምን ያስገኛል ምንስ ያሳጣል? በተቃራኒው አለመጽናትስ? የሚሉና የመሳሰሉ ጥያቄዎች እንዲነሱ ይጋብዛል፡፡
የአንድ ዘመን ልጆች በአንዱ መንደር አድገው፣ በአንድ ክፍል ውስጥ ተምረው …ከጊዜ በኋላ አንደኛው ገበሬ፣ ሌላኛው የጐዳና ተዳዳሪ፣ ከፊሎች ሴተኛ አዳሪ፣ የቢሮ ሠራተኛ፣ መምህር፣ ነጋዴ፣ ባለስልጣን….እንዲሆኑና በደረጃ እንዲለያዩ ምክንያቱ ከመጽናት አለመጽናት ጋር ይያያዛል ወይ? በዓላማው፣ በመርሁና በአቋሙ ፀንቶ የቆየውስ ጽናቱ የጉዳቱ ምክንያት ለምን ይሆናል? ዓላማ በሌለበትስ ጽናት ሲታይ ምን ማለት ይቻላል? ልቦለድ መጽሐፉን ያነበበ እነዚህን ጥያቄዎች ሊያነሳ ይገደዳል፡፡
መጽሐፉ ከሁለት አቅጣጫ እየፈሰሱ መጥተው በአንድ ወንዝ እንደሚገናኝ ውሃ አብረው መጓዝ የቻሉ ታሪኮችን አጣምሮ ይዟል፡፡ አንደኛው በልጅነታቸው የፍቅር ቃል ኪዳን የገቡ ሁለት ወጣቶች፤ ከአስር ዓመት በኋላ አንደኛቸው በሌላኛቸው ዘንድ ያኖሩትን አደራ የማግኘት ፍለጋን ያሳያል፡፡ ሌላኛው፤ በ1960ዎቹ ፖለቲካ ምክንያት ከአገር የወጡ ኢትዮጵያዊያን፤ በስደት ላይ እያሉ ተምረው ዓለም አቀፍ ዕውቅና ያለው ምሁር ከሆኑ በኋላ፤ የማንነት ጥያቄ ሲያታግላቸው ቤተሰባቸውን ፍለጋ ወደ አገር ቤት ቢመጡም መሻታቸው ፈጣን መልስ ሊያገኝ አለመቻሉን የሚጠቁም ነው፡፡
ልቦለዱ የምልሰት ትረካዎቹን ዘመን ሳይጨምር ከ1991 እስከ 1997 ዓ.ም ያለውን ጊዜ የሚያካልል ሲሆን ገፁ ባሕርያቱ በዋነኛነት የሚንቀሳቀሱት በደብረ ማርቆስና በአዲስ አበባ ከተሞች ነው፡፡ የደብረ ማርቆሱ ገፀ ባሕሪያት የልጅነት ታሪክ ብዙ የሚያስደምሙ ጉዳዮችን ይዟል፡፡
በ1980ዎቹ መጀመሪያ ወንዶቹ በረባሶን፣ ሴቶቹ ደግሞ ኮንጐ ጫማን እንደ ብርቅ ያዩ ነበር። በዲጂታል ቁጥሮች የሚሰራም “ዲስኮ” ሰዓት ያለው ልጅ፣ ጓደኞቹን ያስደንቃል፡፡ በከፋይ ጨርቅ የሚሰራው የቻይናዎች የካራቴ ጫማ መጫማት ከፋሽን ተከታይነት በላይም ያስከብራል። ልጆቹ የሽቦ መኪና ሰርተው የሚነዱበት፣ ጭቃ አድበልቡለው ብይ የሚጫወቱበት፣ ተጠራርተው በሸርተቴ ጨዋታ የሚዝናኑበት የተለያዩ ጊዜያት አሏቸው፡፡
ፍሬን፣ ፍሪሲዮንና ነዳጅ መስጫ “ማርሽ ነው”፣ “አይደለም” ብለው በልጅነታቸው በደብረ ማርቆስ ሆነው ከተከራከሩት ጥቂቶቹ በዕውቀት ብቻ ሳይሆን በዕድሜም ጨምረው አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ይገባሉ፡፡ የመጽሐፉ ዋና ገፀ ባሕሪ በርናባስ አንዱ ነው፡፡ የዩኒቨርስቲው ጨዋታና ቀልዳቸው ግን እንደ ትምህርት ተቋሙ ከፍ ያለ ሆኗል፡፡
“ምትኩ ለማቲማቲክስ ልዩና ጥልቅ ፍቅር፣ ረቂቅ ችሎታ አለው፡፡ የሚነገረውን ማንኛውንም ነገር “ማቲማቲካሊ” ነው የሚረዳው፡፡ የሚያስበውም በዚያው በማቲማቲክስ ነው፡፡ ለምሳሌ በዓይን ፍቅር ወድቆላት “ዩቲሊቲ ማክሲማይዘር” ብሎ የሰየማት የአካውንቲንግ የሁለተኛ ዓመት ተማሪ የሆነችው ፍሬሰላም፤ እዚያው ስድስት ኪሎ ዩኒቨርስቲ በር ላይ ታጥፋ መገናኛ ወደሚገኘው ሰፈራቸው ለመሄድ አንዳንዴ የምትይዛትን 64 ቁጥር አውቶብስ ካየ፣ የአውቶብሷን ቁጥር “Two to the power of six” ብሎ ጭንቅላቱ ውስጥ ይመዘግበዋል፡፡”
በቀልድ ፈጣሪነቱ በዩኒቨርስቲው ግቢ ዝነኛ መሆን የቻለው ሸዋፈራሁ ደግሞ “የ R kellyን I Believe I can fly” ዘፈን ወደ አማርኛ ተርጉሞ “አልበር እንዳሞራ ሰው አርጐ ፈጥሮኛል” እንዳለው በሰፊው ተወርቶበታል፡፡ History of Economic Thought ደግሞ “ሥነ ስስታዊ እሳቤ” በሚል ሀገር በቀል ትርጓሜ አስተዋውቋል፡፡”
በደብረ ማርቆስ በአንድ ክፍል ውስጥ ይማሩ ከነበሩት ተማሪዎች ጥቂቶች ለዩኒቨርስቲ በቅተው ወደ ታላቅ ደረጃ የሚያደርሳቸውን መስመር ሲይዙ፣ ከፊሎቹ በተለያዩ ቦታዎች ተበታትነዋል፡፡ ትምህርቱን አቋርጦ ገበሬ የሆነ አለ፡፡ ሌላኛዋ በአዲስ አበባ ከተማ በሴተኛ አዳሪነት ተሰማርታ፣ ደብረ ማርቆስ የሚገኙ ቤተሰቦቿን ትረዳለች፡፡ የልጆቹ ዕጣ ፈንታ፣ ከመጽናትና አለመጽናት ጋር የተያያዘ ነው ወይ? የሚል ጥያቄ እንድናነሳ ይገፋፉናል፡፡
“ሸሌ ተንኮለኛ ካልሆነች ክፉ ወንድ አይገጥማትም” የሚል መደምደሚያ ላይ የደረሰችው ዊንታ የምትባል ገፀ ባሕሪ፤ በችግር ምክንያት ከደብረ ማርቆስ ወደ አዲስ አበባ መጥታ ሴተኛ አዳሪ ለመሆን ያሰበች ጓደኛዋን ለማዳን ብዙ ትለፋለች፡፡ ጥረቷ እንዳልተሳካ ስታይ፤ ጓደኛዋ መልካም እንዲገጥማት ለወንዶች ክፉ እንዳትሆን ትመክራታለች፡፡
ዊንታ በሴተኛ አዳሪነት ሕይወት በኤችአይቪ (ኤድስ) እስከ መያዝ የደረሰ ብዙ ችግርና መከራ ቢገጥማትም አገር፣ ትውልዱንና ሕብረተሰቡን በመታደግ ሥራና ተግባር ላይ እንደተሰማራች የምታስብበት ጊዜም አለ፡፡ በየቤቱ ብዙ ጉድ አለ የምትለው ዊንታ፤ የሚወዳቸው ሚስትና ልጆች ያሉት አባወራ፤ ከቤቱ ያጣውን እኛ ዘንድ ለማግኘት ይመጣል ትልና “በቃ ሰላሙን አግኝቶ ይመለሳል፡፡ ለምን ቢባል፤ ለጊዜያዊ ሰይጣን፣ ለሚያልፍ ስሜት ኑሮውን ይበጠብጣል? እንዲያውም ባይገርምሽ በኛ ምክንያት የስንት ሰው ትዳር ከመፍረስ እንደዳነ?” ትላለች፡፡ እስከዳር ሌላኛዋ የደብረ ማርቆስ ልጅ ናት። በትምህርቷ እስከ ኮሌጅ ዘልቃ በመመረቅ፣ በሙያዋ ተቀጥራ ትሰራለች፡፡ ለወንዶች ያላት አመለካከት፤ ከሴተኛ አዳሪዋ ዊንታ ጋር ሲነፃፀር መቶ በመቶ ፐርሰንት ተቃራኒ ነው፡፡ “የገጠሟትና በቅርበትም የምታውቃቸው ወንዶች ሁሉም ማለት ይቻላል ክፉዎች፣ ራስ ወዳዶች፣ ከጊዜያዊ ደስታ አርቀው ማየት የማይችሉ ወይም የማይፈልጉ፣ ልብ አውልቆች” ብላ ነው የደመደመችው፡፡
እነዚህ ታሪኮች ስለ መጽሐፉ አስተኔ ገፀ ባሕሪያት የተነገሩ ናቸው፡፡ ዋናው ባለታሪኮች በርናባስና እሌኒ ናቸው፡፡ ሁለቱ ወጣቶች በልጅነታቸው የፍቅር ቃል ኪዳን ገብተው ከተለያዩ ከ10 ዓመት በኋላ ሲፈላለጉና ተገናኝተውም በመሟገትና በመካሰስ ቃላቸውን ስለመጠበቃቸውና በጽናት ስለመቆየታቸው በብዙ ገፆች ይተረክላቸዋል፡፡ ደራሲ ትዕግሥቱ ተክለማርያም፤ ስለ ጽናት ምንነት ለማሳየት የሞከሩት የዋናና አስተኔ ገፀ ባሕሪያትን ሕይወት፣ ዓላማና ግብ በንጽጽር በማቅረብ ነው፡፡
የጽናት ምንነት ማሳያ ሆነው የቀረቡት ሌላኛው ባለታሪክ ቤተሰባቸውን ፍለጋ ከባህር ማዶ ወደ አገራቸው የመጡት ምሁርና በዙሪያቸው የሚንቀሳቀሱ ሰዎች ናቸው፡፡ ባለታሪኩ በአንድ ወቅት በጽናት የታገሉለትና ለስደት የዳረጋቸው አመለካከትና አቋም ነበራቸው፡፡ ከስደት ተመልሰው ቤተሰባቸውን ሲያፈላልጉ እና ለአገር ይጠቅማል ባሉት የልማት ሥራ ላይ ሲንቀሳቀሱም ጽናት ይታይባቸዋል፡፡ ያለፈውን ዘመን በሚተቹበት ሃሳብ “ከጥቂት ወራት በኋላ እንዳረጀ ልብስ አውልቀን ልንጥለው በምንችልው ፍልስፍናችን ምክንያት ስንለያይ እንታያለን፡፡
ከዚያም እርስ በእርሳችን መደማመጥ፣ መታገስና መቻቻል እየተሳነን ሄዷል፡፡ ለዚህ ነበር ስንገዳደልና ስንሞት፣ ስንተላለቅ መቆየታችን” እያሉ ያዝናሉ፡፡ ይህ ደግሞ የዛሬ ሀዘናቸውንና የቀድሞ ዘመን ጽናታቸውን እንዴት ማስታረቅ ይቻላል? ማስታረቅ ካልተቻለስ ጽናት ምንድነው? የሚል ጥያቄን ያስነሳል፡፡
ሀንፍሬ የሚባሉት እኚህ ገፀ ባሕሪ ካለፈው ትውልድ በተሻለ በአሁኑ ዘመን ወጣቶች ላይ የተሻለ እምነት ያሳደሩ ይመስላል፡፡ የእውነተኛ ጽናት ማሳያ ምሳሌ ሆነው የቀረቡት በርናባስና እሌኒን የሚያግዙበት አንዱ ምክንያት ይህ ነው ማለት ይቻላል፡፡
ደራሲ ትዕግሥቱ ተክለማርያም፤ በሕብረተሰባችን ውስጥ ያለውን ጽናትና በተቃራኒው ጽናቱን የሚፈታተኑ ብዙ ማሳያና ትርክቶችን አቅርበዋል፡፡ ዋናው ገፀ ባሕሪያት (በርናባስና እሌኒ) ከ10 ዓመት በኋላ ሲገናኙ አንዳቸው ሌላኛቸውን ቃል ኪዳን አፍርሷል በሚል የተፈጠረባቸውን ጥርጣሬ ለማጥራት በምክንያታዊ ክርክር፣ በግልጽ ውይይት፣ በይቅርታና ንስሀ የደረሱበት እውነት ጽናታቸውን አረጋግጦላቸዋል፡፡ የደራሲ ትዕግሥቱ ተክለማርያም እምነትና ተስፋም በዚህ ተንፀባርቋል፡፡ የዛሬ ወጣቶች ለጽናትም ሆነ ለኃላፊነት ተስፋ የሚጣልባቸው ትውልዶች ናቸው ከሚለው በመነሳት መጽሐፋቸውን ያዘጋጁት ይመስላል፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 07 September 2013 10:59

፭ቷ …

ዛሬ ነሐሴ ፴ ነው፡፡
ቀኑ ይበራል አይገልፀውም፡፡
ቀኑን እየተጉመጠመጠ የሚውጠው ወር ከመቼው ከተፍ እንደሚል እንጃ! እንዴት ነው “እሚገፋው … ህይወት … ያለ ምንም ለውጥ? … ጊዜው ሽምጥ ይጋልባል፡፡
እትዬ ንጋቷ በራቸው ላይ ተቀምጠው ሶስት ነገር እያከናወኑ ነው፡፡ በመዘፍዘፊያ ሙሉ የተላጠውን ሽንኩርት ሰተቴ ድስት ውስጥ ከተው የልጅ ልጃቸውን እየጠበቁ ነው፡፡ ተርከክ ብሎ የሚነደው ከሠል ላይ በሸክላ ድስት የጣዱት ሽሮ ወጥ ሙያቸውን ለማሳበቅ ሽታው ሳያንኳኳ ቤቴ ሰተት ብሎ ገብቷል፡፡ ገርበብ ብሎ ከተከፈተው አገልግላቸው ጥጥ መዘዝ እያደረጉ ይፈትላሉ፤ ሳውቃቸው አንድ ሥራ ብቻ ይዞ መቀመጥ አይሆንላቸውም፡፡
በስንጥቁ የቤቴ ቀዳዳ ስመለከታቸው … ወጣቸውን እያማሰሉ … ቀመስ … አድርገው ማማሠያውን ሸክላው ጆሮ ላይ እንደ ጉትቻ አስቀምጠው … መልሰው ወደ ጥጣቸው ተጋቡ፡፡ እሚመጣ እሚገባውን ለመቃኘት ይመስል … ዓይናቸው ከወዲያ ወዲህ ከብለል ይላል፡፡
አቀማመጣቸው በሁለት ተቃኝቷል … እንዝርቱን ለማሾርና ከፍሙ ለመሞቅ በመጠኑ ገለጥለጥ ከፈተፈት ብለዋል፡፡
“ስሚ እንጂ ህብስቴ …” ስሜት ውስጥ ሆኗ ድምጿን ከሳቅ ጋር አሽታ ጠለዘችላቸው … የልጅ ልጃቸው ናት፡፡ “ኩበት እንዲህ የተወደደው ከብቶቹ ተደራጁ እንዴ…? ምነው እቴ … እኔ’ኮ ጨሰስ … ሸተት ሲል ነው ዓውዳመት ዓውዳመት የሚመስለው ብዬ ነው እንጂ በዚህ በኤሌክትሪኩ መጋገር አቅቶኝ አይደለም … የምን ችጋር ማቀንቀን ነው!” የምር ተማረዋል፡፡
“ደግሞ ህብስቴ … የመብራትና የውኃውን መልስ አልሰጠሽኝም፣ እምረሳ መስሎሽ …?” እንደ ስሟ የውኃ ዳቦ የመሠለ ሳቋን እየደወለች ወጣች፡፡
“እማ! ለአለቃ መልስ አይሠጥም እኮ!” ሳቋ ይገርማል፡፡
“ሞኚት… መልስ የማይሠጠው ለገንዘብ ሳይሆን ለአፍ እላፊ ነው፡፡ እኔ ንጋቷ ገንዘብ በዋልጌ ሜዳ ላይ ሲወድቅ አልወድም … ያንገበግበኛል፡፡” ወጣቸውን ጐብኝተው ወደ ጥጣቸው ተመለሱ፡፡
“እማ እንዴት ነው አዲሱን ዓመት በሽሮ እያጨበጨብሽ ልትቀበይው ነው…?”
“እስቲ አምስቷን ቀን ልፁም… ከዚህ በኋላ በላሁ አልበላሁ ለምኔ…! ይልቅ አንቺም ከቻልሽ ፁሚ…”
“ማ… ምን በወጣኝ … ኑሮ ራሱ ፆም አይደል…!” መንቀርቀር አለች፡፡
“አይ ሞኝት … ሳይጐድልበሽ መፆም መፀለይ ያልቻልሽ… ላንድ ሳምንት ብትቸገሪ … ጌታችንን ድጋሚ ትሰቅይዋለሽ፡፡”
“ኧረ በስመዓብ በይ እማ!”
“ይሁን እስቲ … በይ ከኛ ጓሮ ካለው ኮባ ሁለት ቁረጭና ለሸንኮሬ ውሰጅላቸው… እንዳትረሺ! አሁን ይሔን ሽንኩርት ቶሎ አስፈጭተሽ ነይ …”
“እማ!” ተገርማለች፡፡
“ፍሪጅ ውስጥ ይቀመጣል … የምን ሲደርስ መንደፋደፍ ነው … ዶሮዎቼንም ገለታ ባርኳቸው አጣጥቤ እከታለሁ”
በረጅም ገመድ የታሰሩት ሁለት ቀያይ ድምድም ዶሮዎች የሰሙ ይመስል በተራ በተራ ኩኩሏቸውን አስነኩት፡፡
አንገቴን ብቅ አድርጌ ሳያቸው … “አጅሬው ምነው ሰጐን ይመስል አንገትህን አሠገግህ…?” አሉኝ፡፡
“ደህና አደሩ እትዬ ንጋቷ …” ሙሉ በሙሉ ወጥቼ በሬ ጋ ቆምኩ፡፡
“ደህና አረፈዱ በሚለው ይታረም!” ቀይ ፊታቸው ላይ ፀሐይ የወጣች ይመስላል … አንገታቸው በንቅሳት ስቋል … ግራና ቀኝ እጃቸው አይበሉባው ላይ ወደል ወደል መስቀል አለ፤ ነጭ ሻሽ የመሠለው ጥርሳቸው በአረንጓዴ ከተወቀረው ድዳቸው ጋር ተዳምሮ እንኳን ስቀው ፈገግ ሲሉ ልብ ወከክ ያደርጋሉ፡፡ እንዲህ ዕድሜአቸው ገፍቶም ቀሽት ናቸው፤ ይብላኝ ልጅ እያሉ…!
“እንደምን አረፈዱ …” ስህተቴን ሳልረሳ ማረም ነበረብኝ፡፡
“እናትና ልጅ ክብር ይግባቸው፡፡ ከዘመን ዘመን እንደ አደይ አበባ ያልዘለለኝ አንድዬ ምስጋና ይድረሰው”
ማርያምን ሲወዷት አይጣል ነው፡፡ “ልጅም፣ አምላክም የወለደች ብቸኛ!!” እያሉ ይገረሙባታል፤ በመታደሏ፡፡
“አሜን” ዋናው እሱ ነው፤ ይመስላል አባባሌ - መሬት መሬቱን እያየሁ፡፡
“ምነው አቀረቀርህ …?”
“እ…ምንም”
“ደግሞ ምንድነው ከወንድምህ ጋር የምትናቆሩት…?”
“ኧረ እትዬ ንጋቷ ሊደፋኝ ነው…! ተሳስቼ ኪሴ ውሰጥ ሳልደብቀው ገንዘብ ካደረ … ገላውን ቀዶ ነው መሠለኝ የሚደብቀው አላገኘውም፡፡ ማታ ለዛ ነው የተጣላነው … በዛ ላይ ጥምብዝ ብሎ መጣ፡፡”
“ስማ ሃምሣ ብር ጠፋብኝ ብለህ ነው እንደዚህ አንድ ክፍለ ከተማ የተቀማህ ይመስል የምታቅራራው?!” በሩን በርግዶ ገፍቶኝ ወጣ፡፡ እትዬ ንጋቷ ጥሎባቸው ይወዱታል፡፡ “የህብስትን አባት ያስታውሠኛል፤ እንደሱ ቦጅቧጃ ነው” ስለሚሉ እሱም አይፈራቸውም፡፡
“ለምን አርፈህ አትወጣም … የተሰረቅሁት እኔ፣ የምትቆጣውና የምትሳደበው አንተ…” ታላቁ ነኝ፡፡
“አታካብዳ…!”
“ሠይጣን አሚር ጠጣ እሺ!”
“አፈር ብላ አንተ ቀውላላ፣ አማረብኝ ብለህ ነው ወንድምህን አሚር ጠጣ ብለህ የጋበዝከው … የኔ ሾላ እኔ ጉሽ ጠላ እሠጥሃለሁ…” በስስት ተመለከቱት፡፡
“ለነገሩ ሾላዬ ላንተኮ ዐፈር በጥብጠው ቢሠጡህ ትጋተዋለህ…”
ወንድሜ አቀረቀረ፡፡
“እየው ሾላዬ እንደው ስሞትልህ… እቺ ማታ እያመሸህ፣ በዛ ላይ ያማረብህ መስሎህ እያላዘንክ የምትመጣውን አቁም!” እንዳቀረቀረ … እራሱን በአዎንታ ነቀነቀላቸው፡፡
“ስጠኛ…?” ቀስ ብዬ ጠየኩት፡፡
“ምንድነው የምሠጥህ…?!” እሳቸው እንዲሠሙት ይመስላል አጯጯሁ፡፡
“ሌላው ቢቀር ለምንድነው የማታግዘኝ?”
“ምን ተሸከምክና?”
“አንተን መሸከም በራሱ … ሙሉ መጋዘን ብረት መሸከም እኮ ነው!”
“ታቅራራለህ እንዴ …” መላጣውን እያሻሸ … በቆረጣ እትዬ ንጋቷን ይመለከታል፡፡
“አትቀልድ! የትምህርት ቤት ክፍያ አለ … ቀለብ … ጋዝ አልቋል … እንዳየኸው አምስት ኪሎ ቲማቲም ሁለት ቀን ሳንጠቀምበት ተበላሽቶ ተጣለ፡፡ አንተ ፀሐይ ላይ ማውጣት ሰንፈህ አምስት ኪሎ ሽንኩርት በቀለ፣ በሰበሠ፣ ይሄ ሁሉ ብክነት አያሳዝንህም?” እትዬ ንጋቷ ዝም ብለው ጥጣቸውን እየፈተሉ ይሠማሉ፡፡
“እሺ አሁን ለምሣ ሰላሣ ብር ሥጠኝ?”
“አላበዛኸውም… እዚህ መጥተህ አትበላም … ወይ ቋጥረህ አትወጣም!”
“ማታ ስታላዝን መች ሰራህ!”
“ተው! ተው! እንተጋገዝ… አሁን በአስር የቤት ኪራይ አለ … ይሔ ሁሉ እኔ ጫንቃ ላይ ነው ያለው፡፡” ጆሮው ጋ ጠጋ ብዬ … ቀስ ብዬ ነበር በእርጋታ …
“እና መቻል ካልቻልክ ለምን አመጣኸኝ?!”
“ሰው ትሆናለህ ብዬ ነዋ! ኑሮን የምታግዘኝ መስሎኝ … ተምረህ እንድትለወጥ ጓጉቼ …” ተወራጨሁ፡፡ በጣም ተሠማኝ … ድግግሞሽ ህይወት ያስጠላል፡፡
“አገር እንደሚቀልብ ሰው አቅራራህ!”
“አሚር ጠጣ!” በጣም አናደደኝ፡፡
“ቱ… አፈር ብላ! አፈር ያስበላህ …! ምነው አንተ … እርጐ የጋበዝከው መሠለህ እንዴ … አስር ጊዜ አሚር ጠጣ የምትለው፤ ደግሞ ከየት ያመጣኸው ስድብ ነው … ያለወትሮህ …”
“ምን ላርግ እትዬ ንጋቷ … ሊያሳብደኝ ነው … አቃጠለኝ እኮ!”
“ቢሆንም ቀስ አድርገህ ምከረው…”
“ይሔ ብነክረውም አይርስ…!”
“አትሠልች… እንዳንተ ስራ እንዲወድ … እንዲያነብ … ቀስ እያልክ …”
“ኧረ ይሔ መጽሐፍ ገልጦ ከሚያነብ … የሴት ቀሚስ መግለጥ ይቀለዋል…!”
“እሱስ ተወው … ከማን ያየውን…”
ቀስ ብሎ ሳቀ፡፡ ህብስትም ለምን እንደሳቀች ሳላውቅ ከውስጥ እየተፍነከነከች ወደ እኛ መጣች፡፡ ወንድሜ መላጣውን እያሻሸ ሊወጣ ሲል … “ገለታ… መታጠፊያው ድረስ አግዘኝ…?” ድስቱን ጆሮና ጆሮውን አንጠልጥለው እንደ ባለጌ ህፃን ወጡ፡፡
“አየኸው የዋህ እኮ ነው…” እባኮት ሥለሚወዱት ነው … አልኩኝ በሆዴ፡፡ ቤት ገባሁና ቁልፍ ይዤ … በሩን ቆልፌ ልወጣ ስል…
“እ…እየውልህ… አምስቷን ቀን መስከረም አስር እምትሠጠኝ ላይ ደምረህ ሥጠኝ…!” ወገቤ ለሁለት የተከፈለ መሠለኝ፤ እንደ ማቅለሽለሽም አደረገኝ፡፡
“ማለት … ጳጉሜን ደምረዋት ነው…?”
“አዎ… አስራ ሶስት ወር ያላት ሐገር እያላችሁ ትፎልሉ የለም እንዴ”
“አምስት ቀን እኮ ናት”
“አንድም ቀን እድሜ ነው”
“እሱማ አዎ … ግን … የትም ቦታ እኮ ሒሳብ ላይ አይደመርም…”
“እንግዲህ የእኔን ቤት ከየትም ቦታ ጋር ከደመርከው ስህተት እየሰራህ ነው”
“አይደለም እኮ እትዬ ንጋቷ … መንግስት መስሪያ ቤትም ቢሆን እኮ አምስቷ ቀን ሒሳብ ላይ አትደመርም…”
“መንግስትን ተወው! ሌባ ስለሆነ ነው፡፡” ሊሆን ይችላል አልኩ በሆዴ፡፡
“እግዜርም ቢሆን እድሜአችን ላይ መች ይደምረዋል…” ለማራራት አስቤ ነበር፡፡
“እሱ ሞልቶት ስለተረፈው ነው”
“ምን…?”
“አንድዬ የእድሜ ካዝናው ሙሉ ስለሆነ እኛ ጉዳይ ውስጥ አትጥራው፡፡”
“ለዚህ ከባድ ጉዳይ እሱን ያልጠራን ማንን እንጠራለን?”
“እንግዲህ ተናግሬአለሁ … አምስቷን ቀን ደምረህ እንድታመጣ ብሬን! አይ የለኝም … የምትል ከሆነ … አምስቷን ቀን ከወዲሁ ብትቀንስ … ከወዲያ መስከረም አምስት ቤቴን ለቀህ እንድትወጣ!” ጭው አለብኝ፡፡ በዚህ የኑሮ ግለት … በዚህ የቤት እጦትና የኪራይ መወደድ ከዚህ ቤት ወጥቼ የትስ አገኛለሁ … እንዴትስ ከአቅሜ ጋር የሚመጣጠን ቤት ይገጥመኛል፡፡ አንገቴ ተቀንጥሶ ሊወድቅ መሠለ …
“አንተ ቀውላላ…”
“አቤት…”
“ምነው ተለጐምክ… ሥራ እየሰራሁ ነው አላልከኝም?… ይሔ ቲያትር ነው … ደግሞ ሩጫም ሮጣለሁ … አላልከኝም…? ሁለቱም እኮ ብራሞች ናቸው፡፡”
“አዎ” ቃላቱን መዘዝኩት፡፡
“እና… እምትሮጠውና ቲያትርህንም ደግሞ የደበቅኸኝ ፊልምም፣ ሴቶቹ ላይ ነው እንዴ የምትሠራው…? ልጄ መንገድ ላይ ባየሁህ ቁጥር ሴት አቅፈህ ነው፣ ትከሻህ አለመገንጠሉ … ትገለፍጣለህ … ጥርስህ አለመርገፉ፣ ህልምህን እየተገበሩልህ ይመስል ደግሞ … በየመንገዱ የተለጠፈው ፎቶህ ሳይቀር … ሴቶቹን አቅፈህ ነው … ምን አቅፈህ ብቻ … እያፈስክ ነው የሚመስለው፡፡” መሳቅ አማረኝ … ግን ከሳቅሁ እንባዬም እንደሚመጣ ገባኝ … አፈርኩ፣ ጥጣቸውን አስቀምጠው … በአነጋገራቸው የጠወለገውን ፊቴን ተመለከቱ…
“እህ… ምን አሠብክ…? የአምስቷን ቀን?”
“ኧረ… ፈጣሪም አይወደው … ምነው… ጠበል እንኳ በነፃ አይደለም እንዴ የምንጠመቀው…”
“እስቲ ሩፋኤልን በል…?” እሚያላግጡም መሠለኝ … ግን አይደለም፡፡
“እግዚአብሔርን…” አሁንም አተኩረው ተመለከቱኝ… ከምስኪን ፊቴ ላይ የሚያነቡት የሐዘን ደብዳቤ ያለ ይመስል፡፡
“እና አሁን ኑሮውን አልቻልኩም … ሥለዚህ የለኝም ነው የምትለው?!”
“አ…ዎ…” ቃላት ከጉሮሮዬ መውጣት አቃታቸው፡፡
“ምነው በከተማው ፎቶህን ከተለያዩ ሴቶች ጋር ተለጥፎ አየው የለም!”
“ምን… ያው… እያሰሩ እኮ አይሠጡንም…! እስክንሠራላቸው እንጂ ከዛማ … እኛ መለመን ሲገባን … እኛው ለማኞች ሆንን”
“ስራውንም የለማኝ አስመሰላችሁት … ቢሆንም … ህሊናህ ውስጥ ብስለት ካለጠፍክ … የከተማው ፎቶ ዋጋ የለውም፡፡ ጠዋት ያንተ ተለጥፎ ከሠዓት ደግሞ እንዳንተ ሴት ያቀፈ እላይህ ላይ ይለጠፋል፡፡ ምነው እንደዛ ባናት ባናቱ ከምትለጣጠፉ … አጠገብ ላጠገብ ብትሆኑ…”
“ያው… ሥሥታሞች አይደሉ … አንዱ ባንዱ ትከሻ ላይ መበልፀግ ይመኛል”
“አትሞኝ ላብህ የትም አትቀርም … በላብህ ያላገኘሀትን ገንዘብ ደግሞ ከሥር ከሥር በይ ያዝበታል” እኚህ ሴትዮ አንዳንዴ የሚያስደነግጥ ሐሳብ ይሠነዝሩብኛል … የቡጢ ያህል፡፡ እኔ ለራሴ ጭው እያለብኝ ነው፡፡ ሐሳባቸውን ሳላስጨርስ ልወጣ ስል …
“እና ምን ወሠንክ…?”
“እትዬ ንጋቷ … እስከዛሬም … ፍቅርዎትን … ነፃነትዎን ብለን የተቀመጥነው ኪራዩን ስለቻልነው ሳይሆን እናትነትዋ በልጦብን ነው፤ ስለዚህ … በቃ … እግዚአብሔር ያውቃል … ሌላ ቤት እፈልጋለሁ…” መራመድ ጀመርኩ፡፡
“ና…ና…” አይናቸው ውስጥ እንባ ይዋኛል፡፡ አቀረቀሩ… ደግሞ ቀና አሉ …
“ልጄ… ይሔ ልብስ እና እቃ ስትገዙ … የሚለጠፈው ታናሽ ታላቅ ነው… ምንድን ተብሎ የሚለጠፈው?”
“ታላቅ ቅናሽ?” ፊቴን ዘፍዝፌዋለሁ፡፡
“እህ … ላንተም ልዩ ታላቅ ቅናሽ አድርጌልሐለሁ” ልቤ ሆያ ሆዬ ደለቀች … አብዝቼ ፈራሁ… እንደ ፍቅር የሚያስፈራ ነገር የለም፡፡
“ኧረ እትዬ ንጋቷ … የምርዎን ነው?…”
“ስቀልድ ነው የኔ ልጅ … እኔ ክው ልበል … የእኔ ፊት ማድቤት ይምሠል… ልጄ ባዲሱ ዓመት ከምትሰጠኝ ላይ መቶ ሃምሣ ብር ቀንሼልሃለሁ … አንተ ደግሞ … መልካም ሥራህና ጥሩነትህ ይብዛ…! እምታንጠለጥላቸውን ሴቶች ደግሞ ቀነስ አድርግ! ካላወክበት አንዷም ሸክም ናት!”
በርከክ ብዬ ለእንዝርትና እና ለፍሙ የተገለጠውን ጉልበታቸውን ሳምኩ፡፡ ጣታቸውን ሰደው … ፀጉሬን ዳበሱኝ፣ እንባዬ አመለጠኝ… ጉልበታቸውን ለብ ያለ ነገር ሲዳብሳቸው …
“ምነው ልጄ … እንድታለቅስ እኮ አይደለም … የወንድምህን አመል ስለማውቅ፣ ኑሮውም ስለሚገባኝ … በዛ ላይ ስንት አመት ሙሉ አንገትህን ደፍተህ ትወጣለህ፣ አንገትህን ደፍተህ ትገባለህ … በሚገባ አክብረኸኛል … የማርያም ልጅ ያክብርህ፡፡ ለልጄም ወንድሞቿ እንጂ ሌላ ምኗ ነበራችሁ … እሰልል ነበር እኮ … የደረሠች ሴት ያለው መች እንቅልፍ ይተኛል። እዚህ ጊቢ መኖራችሁ በራሱ ለእኔ ክብር ነው፤ ለዛ ነው ልጄ እንደልቤ የምሆንባችሁ … እስቲ ያንዱን ችግር እንደራስ ችግር አድርገን እንተጋገዝ … እኔ ሞልቶኝ … እኔ ስቄ ስኖር … የሌላው ርሃብና እንባ … ድሎት ይሆነኛል…? አይሆነኝም፡፡ ልባችን አደይ አበባን ይሁን … ወቅት ጠብቆ ብቻም ሳይሆን ተኝተን ስንነሳ በነጋ ቁጥር ሁሌም ንፁህ ልብ ይኑረን … ማነው ‘አቤቱ ንፁህ ልብ ፍጠርልኝ’ ያለው … እንዲህ ነው ህይወትን መለመን፤ እምንካፈለው ችግር እና እምናካፍለው አያሳጣን ፈጣሪ … ያኔ መድኃኒያለም ጉልበቱን አይነፍገንም፡፡ አብሮ መሳቅማ በደስታህ ጊዜ ማንም መንገደኛ ያጫፍርሃል … እና ልጄ የምሬን ነው፡፡ በህይወት እስካለሁ ሲከፋችሁ ይከፋኛል … ሲርባችሁ ይርበኛል፡፡ አንተ በርትተህ ካየሁህ … የወንድምህን ነገር ለኔ ተወው… እቀይረዋለሁ… ምንም የተሻለ ነገር ሳይኖር “ተው! ተው!” ከአድርግ አይተናነስም”
በደንብ ቀና ስል … እንባዎቼን በቀኝ እጃቸው አበሱልኝ … ዶሮዎቹ … እኩል በሉ የተባሉ ይመስል … “ኩኩሉ” አሉ፡፡
በዶሮኛ … “እድሜዎት ይርዘም” መሠለኝ፡፡

Published in ልብ-ወለድ
Page 13 of 16