Saturday, 01 August 2015 14:24

ውሸትና ሮቦት…

“ውሸት ስንናገር በጥፊ የሚያጠናግር ሮቦት በየቦታው ይተከልልንማ!”
                    
   እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ስሙኝማ… የመዋሸት ነገር ካነሳን አይቀር…ይቺን ስሙኝማ… አባት ሆዬ ማንም ሰው ውሸት በተናገረ ጊዜ በጥፊ የሚያጮል ሮቦት ይገዛል፡፡ ከዛም አንድ ቀን እራት ላይ ሊሞክረው ይወስናል። አባትየውም ልጁን “ከሰዓት በኋላ የት ነበርክ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ልጁም…
“ትምህርት ቤት ነበርኩ…” ይላል፡፡
ሮቦቱ በጥፊ ያጮለዋል፡፡
ልጁም … “ጓዷኛዬ ቤት ቪዲዮ እያየሁ ነበር፡” ሲል አስተካከለ፡፡ አባትየውም…
“ምን አይነት ፊልም አየህ?” ይለዋል፡፡
“የካራቴ…” ምናምን ብሎ ሲጀምር ሮቦቱ ደግሞ በጥፊ ያጮለዋል፡፡
ልጅየውም ጣደፍ ብሎ…“እሺ፣ የወሲብ ፊልም ሳይ ነበር…” ይላል፡፡ አባትየው ቆጣ ይልና…
“እኔ በአንተ ዕድሜ ሳለሁ እንዲህ አይነት የብልግና ፊልም አይቼ አላውቅም…” ይላል፡፡
ሮቦቱ በጥፊ ያጠናግረዋል፡፡
ይሄን ጊዜ እናትየው ከት ብላ ትስቅና… “ምን ያድርግ ምንም ቢሆን የአንተ ልጅ አይደል…” ትላለች፡፡
ሮቦቱ በጥፊ አጠናግሯት አረፈላችሁ፡፡
ውሸት ስንናገር በጥፊ የሚያጠናግር ሮቦት በየቦታው ይተከልልንማ!
ኮሚክ እኮ ነው…ብዙ ጊዜ በአንድ ጉዳይ ላይ ሁለት የተለያዩ ነገሮች ሁለቱም እውነት ሊሆኑ አይችሉም አይደል! ለምሳሌ ይህ ‘አምደኚስት’ ወይ አጭር ነው፣ ወይ ረጅም ነው። አጭርም፣ ረጅምም የሚሆንበት ተአምር ገና አልተከሰተም፡፡ (‘ገለጻ’ ተሰጥቶ ልብ ውልቅ አይነት ነገር አይመስልም!) ዘንድሮ ግን “አጭር ነው…” የሚለውም ‘እውነት’ ነው፣ “ረጅም ነው…” የሚለውም ‘እውነት’ ነው፡፡ በቃ…እንዲህ ስንሆንስ! እኛ ዘንድ በአንድ ጉዳይ ላይ የተሰጡ አሥር የተለያዩና የማይገናኙ ነገሮች ‘እውነት’ ይሆናሉ፡፡ ልክ ነዋ… ሁላችንም እውነተኛ “…እኔና እኔ ብቻ…” እያልን ነዋ!
ውሸት ስንናገር በጥፊ የሚያጠናግር ሮቦት በየቦታው ይተከልልንማ!
አንድ ቄስ የሳምንቱን ጉባኤ ሲጨርሱ እንዲህ ይላሉ፡፡ “በሚቀጥለው እሁድ ስለሚዋሹ ሰዎች እናወራለን፡፡  ለእሱም ለመዘጋጀት ሁላችሁም የማርቆስ ወንጌል ምዕራፍ አሥራ ሰባትን አንብባችሁ ኑ፣” ይላሉ፡፡
በተከታዩ እሁድ አዳራሹ ጢም ይላል፡፡ ቄሱም… “ባለፈው ሰንበት እንዳልኳችሁ የማርቆስ ወንጌል ምዕራፍ አሥራ ሰባትን አንብባችሁ እንደመጣችሁ እምነቴ ነው፡፡ ስንቶቻችሁ ናችሁ ያነበባችሁት?” ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡
ተሰበሳቢዎቹ በሙሉ እጃቸውን ያወጣሉ፡፡ ቄሱ ምን አሉ መሰላችሁ…
“ዛሬ ስለ እናንተ ነው ማውራት የፈለግሁት። የማርቆስ ወንጌል ምዕራፍ አሥራ ሰባት የለውም።”
ውሸት ስንናገር በጥፊ የሚያጠናግር ሮቦት በየቦታው ይተከልልንማ!
እናላችሁ…ውሸትና እውነቱ እየተደበላለቀ ግራ ተጋብተናል፡፡ የምር እኮ የማይዋሽ ማግኘት አስቸጋሪ ሆኗል፡፡ ነው…ወይስ የውሸት ትንታኔ ተለውጧል! የምር እኮ… እኛም ‘ውሸት’ በምንሰማበት ጊዜ ደማችን ‘አናታችን ላይ መውጣቱ’ ቀረ መሰለኝ፡፡
ስሙኝ የደምን አናት ላይ መውጣት ካነሳን አይቀር ይቺን ቀልድ ቢጤ ስሙኝማ…አንድ ሀኪም ታካሚውን “ጌታው ከፍተኛ የደም ግፊት አለብህ፡፡ ከቤተሰብ የወረስከው ነው?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
ታካሚውም… “ይመስለኛል…” ይላል፡፡ ዶክተሩም…
“ከአባትህ ወገን ነው ከእናትህ ወገን?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
ታካሚውም “ኧረ ከሚስቴ ቤተሰብ ወገን ነው!”  ይላል፡፡ ዶክተሩም ግራ ይገባውና…
“እንዴት ነው ከሚስትህ ቤተሰብ ወገን የደም ብዛት በሽታ የምትወርሰው?” ይለዋል፡፡ እሱዬው ምን ቢል ጥሩ ነው…
“ዶክተር፣ የሚስቴን ቤተሰቦች ስላላየኻቸው ነው እንዲሀ የምትለው፡፡”  አሪፍ አይደል፡፡ የምር ግን አማቶች ባይኖሩ ኖሮ ባልና ሚስት ማንን ‘ይረግሙ‘ ነበር!
እናላችሁ….እውነትና ውሸት እየተቀየጡ መለየት ቸግሮናል፡፡
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ነገሬ ብላችሁ እነኚህ ‘ታላላቅ’ የዜና ማሰራጫዎች የሚያሰሟቸውን ዜናዎች አዳምጡማ፡፡ ፈረንጆች… “በመስመሮች መሀል ማንበብ…” የሚሏት ነገር አለች አይደል… ‘በመስመሮች መሀል’ አዳምጡማ! በተመሳሳይ ዜና ላይ የተለያዩ ‘መረጃዎች’ ይሰጧችኋል፡፡ አለ አይደል… የዩክሬይኑን ተኩስ ማቆም ስምምነት ያፈረሰችውን የመጀመሪያ ጥይት የተኮሱት ወይ አማጺዎች ናቸው ወይ የመንግሥት ወታደሮች ናቸው፡፡
አንዱ “አማጺዎች” ሲል ሌላው “የመንግሥት ወታደሮች” ካለ…አለ አይደል…አንደኛቸው ‘ዋሽተዋል’ ማለት ነው፡፡ ለነገሩ ዘንድሮ ዜና ‘የሚዘገበው’ እንደ ሚዲያ ተቋማቱ ‘ፍላጎት’ ከሆነ ሰንብቷል፡፡
የምር ግን አሁን በእኛ ሚዲያዎች ላይ ‘እውነት’ና ‘ውሸት’ ይለይ ቢባል… ራሱን የቻለ ግብረ ኃይል ባያስፈልግ ነው! አሁን፣ አሁንማ ደረትን ነፍቶ ‘ውሸት’ መናገር የጥበብ ጉዳይ እንጂ የ‘አጉል ባህሪይ መለያ’ መሆኑ ቀርቷል፡፡
አንድ ጊዜ አንድ ሙዚቃ ዝግጅቶች ነገር የሚወድ ወዳጃችን ሲያጫውተን የሆነ ዝግጅት  ላይ ‘ሰርፕራይዝ’ እንግዳ ይኖራል ምናምን ተብሎ አይደለም ‘ሰርፕራይዝ’ እንግዳ በመደበኝነት ይመጣሉ የተባሉት እንኳን ሁሉም አልመጡም፡፡
እናላችሁ…በተለይ እንዲህ አይነት ነገሮች ላይ ችግሮች አሉ፡፡ ይመጣል የተባለው ‘ሰርፕራይዝ’ እንግዳ ስሙ ሲጠቀስ እኮ ራሱም ‘ሰርፕራይዝድ’ ሊሆን ይችላል! እናላችሁ…ውሸት በዝቷል፡፡
የ‘ሰርፕራይዝ’ ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ስሙኝማ…እሷዬዋ ባሏን ‘ሰርፕራይዝ’ ማድረግ ፈልጋለች፡፡ እናላችሁ… አንድ ቀን ማታ ከሥራ ሲመለስ በጣም ስስ የሆነ ፒጃማ ለብሳ ሶፋ ላይ ተቀምጣ ጠበቀችው፡፡ ነገርዬው ያልተለመደ ስለነበርም እሱዬውም…
“ዛሬ እንዴት ነው፣ ፏ ብለሻል!” ምናምን ብሎ ይቀላልዳል፡፡ እሷዬውም…
“ዛሬ ያዘጋጀሁልህን አታውቅም…” አለችው፡፡
“ምንድነው ያዘጋጅሽልኝ?” ይላታል፡፡ እሷም…
“መኝታ ቤት እንሂድና እጅና እግሬን ግጥም አድርገህ ከብረቱ ጋር አስረህ የፈለግኸውን ማድረግ ትችላለህ…” ትለዋለች፡፡
እንደተባለውም መኝታ ቤት ይሄዱና እጅና እግሯን ግጥም አድርጎ ያስራታል፡፡ ከዛላችሁ…እንግዲህ የፈለግኸውን አድርግ ብላው የለ… ቢራ አምሮት ኖሮ ወደ መጠጥ ቤት ሄዶላችሁ አረፈው፡፡
እንትናዬዎች… እንትናዎቻችሁን ‘ሰርፕራይዝ’ ለማድረግ ስትፈልጉ ከአልጋ ጋር መታሰር የሚለውን እንዳታስቡት፡፡
እግረ መንገዴን ይቺን ስሙኝማ…ሚስትየዋ ውሻዋ “ተቀመጭ…” ስትባል ቁጢጥ ብላ እንድትቀመጥ እያለማመደቻት ነው፡፡ ግን እንደፈለገችው ቶሎ ሊሰካላት አልቻለም፡፡ ይህን ያየው ባል ሆዬ ምን ይላታል…
“የእኔ ፍቅር፣ እንዲሳካልሽ ከፈለግሽ ተስፋ ሳትቆርጪ…” ሲል እሷ አቋርጣው ምን ብትለው ጥሩ ነው…
“ግዴለም አትንገረኝ.. እንኳን ቡቺን አንተም መጀመሪያ ላይ እንዲሁ ነበር ያስቸገርከኝ…” ብላ ከውሻ ጋር በአንድ ዓረፍተ ነገር ውስጥ ከትታው አረፈች!
እናላችሁ… ስለ ውሸት ስናወራ…አሁን አሁን ብዙ ማስታወቂያዎች ከ‘ማርኬቲንግ’ ዘዴነት ይልቅ…አለ አይደል… ወደ ‘ውሸትነት’ ይጠጋባችኋል፡፡  ምሽት አንድ ሰዓት ሳይሞላ ከሰለቸው ዘበኛው በስተቀር አንድም ሰው በማይገኝበት የህክምና ተቋም… ‘የሀያ አራት ሰዓት አገልግሎት’ አይነት ‘ፕሮሞሽን’ ብልጥነት ሳይሆን ‘ውሸት’ ነው፡፡
ውሸት ስንናገር በጥፊ የሚያጠናግር ሮቦት በየቦታው ይተከልልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

  ከህንድ ጦርነቶች በአንዱ እንዲህ ሆነ አሉ፡፡
የፈረሰኛው ብርጌድ የወራሪዎቹን ጐሣ ድባቅ መታና ደመሰሰ፡፡ የተረፈው የጐሣው መሪ ብቻ ነበር፡፡
የፈረሰኛው ብርጌድ አለቃ ለተረፈው መሪ እንዲህ አለው፡-
“እጅግ አድርገህ በጀግንነት ስለተዋጋህ ነብስህን አተርፍልሃለሁ - አልገድልህም!”
ያም የወራሪዎቹ ጐሣ መሪ፤ ስለተደረገለት ምህረት ምሥጋና ለማቅረብ ቃላት ሲፈልግ ሳለ፣ ከተራራው አናት መዓት የህንድ መንጋ መጥቶ የፈረሰኛውን ብርጌድ ይደመስሰዋል። የተረፈ አንድ ሰው ቢኖር የብርጌዱ አለቃ ብቻ ነው፡፡ አሁን እንግዲህ ቦታ ተለዋወጡ - የብርጌዱ አለቃና የወራሪዎቹ መሪ፡፡
የወራሪዎቹ መሪ ለተረፈው የብርጌዱ አለቃ በፈንታው እንዲህ አለው፡-
“እኔ እንዳንተ ደግ አልሆንልህም፡፡ ሞት አይቀርልህም፡፡ ግን ሦስት ምኞት እንድትናገር እድል እሰጥሃለሁ”
የብርጌዱ አለቃም፤
“የመጀመሪያ ምኞቴ፤ ፈረሴን ለማየት እንድትፈቅድልኝ ነው” አለ፡፡ ተፈቀደለትና ፈረሱ መጣለት፡፡ ከዚያም የብርጌዱ አለቃ ለፈረሱ የሆነ ነገር በጆሮው ሹክ አለው፡፡ ፈረሱ ፈረጠጠ፡፡
ይሄኔ የብርጌዱ አለቃ፤ “ትንሽ እንጠብቀው” አለ፡፡
ተፈቀደለት፡፡
ዕውነትም ፈረሱ ከአንድ ሰዓት በኋላ ተመለሰ፡፡ አንዲት በጣም ውብ የሆነች ልጃገረድ ይዞ ነው የመጣው፡፡
የብርጌዱ አለቃ ለጐሣው መሪ፤
“ይቺን ልጀገረድ ሰጥቼሃለሁ” አለው፡፡
የወራሪዎቹ መሪ ልጃገረዲቱን ወስዶ ፍቅሩን ገልጦላት ተመለሰና፡-
“ሁለተኛው ምኞትህ ምንድን ነው?” አለው፡፡
የብርጌዱ አለቃም፤
“ፈረሴ ይምጣልኝ” አለ፡፡
ተፈቀደለትና ፈረሱ መጣለት፡፡
አሁንም በጆሮው የሆነ ነገር ሹክ አለው፤ ፈረሱ ጋለበ፡፡
“ትንሽ እንጠብቀው” አለ አለቃ፡፡
ፈረሱ ከአንድ ሰዓት በኋላ ሌላ ምን የመሰለች ቆንጆ ልጅ ይዞ መጣ፡፡
አለቃም ለጐሣው መሪ፤
“ይቺንም ልጅ መርቄ ሰጥቼሃለሁ” አለው፡፡
የወራሪዎቹ ጐሣ መሪ ልጅቱን ወሰደ፡፡ ሲዝናና ቆይቶ ተመለሰና፤
“ሦስተኛው ምኞትህስ ምንድን ነው?” አለው፡፡
“ፈረሴን እንዳገኘው ይፈቀድልኝ”
ተፈቀደለትና ፈረሱ መጣ፡፡
የብርጌዱ አለቃ ፈረሱ ላይ ወጣ፡፡ እርካቡን ኮለኮለና መጭ አለ፡፡ ማን ያስቁመው? ለዐይን ተሰወረ!
*                  *                     *
ከጉልበተኝነት ብልህነት ይበልጣል፡፡ ደግ ላደረጉልን ክፉ መመለስ መበለጥ እንጂ መሻል አይደለም፡፡ ምኞቶቻችን ተጨባጭ ይሁኑ፡፡ ተጨባጭ ቢሉም ለሀገርና ለህዝብ ፋይዳ ያላቸው ማለት ነው፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ ምድራዊ ገነት ብትሆንልን ማንም የሚጠላ የለም፡፡ ሆኖም ምኞታችን አቅማችንን ያገናዘበ ሊሆን ይገባዋል፡፡ በብዙ ጉዳዮች ከልኩ በላይ መወጣጠር (Over - stretched እንዲል) መሰነጣጠቅም ሆነ መሰባበርን ማስከተሉን እንገነዘባለንና፡፡
“ሲያርስ ነካክቶ፣ ሲዘራ አፈናጥሮ፣ ጥፋተኛ እኔን አድርጎ” የሚባል ተረት አለ፡፡ በቅጥ - በቅጡ ያልሰሩት ሥራ፣ በአግባቡ ያላዘጋጁት ነገር፤ በኋላ ሰበባችንን በሌሎች ላይ እንድንላክክ ያደርገናል ማለት ነው፡፡ ሁሉንም መነካካትም አንዱን ሳናበስል እንድንቀር ያደርገናል፡፡ የጎረቤቶቻችንን አያያዝ በተመለከተ አንድም በዲፕሎማሲ መስክ፣ አንድም ሉዓላዊነትን በማስከበር ረገድ፤ አሳምረን መጓዝ ያስፈልገናል፡፡ የኃያላን መንግሥታትን ድጋፍ የማይሻ አንድም የሶስተኛው ዓለም አገር ባይኖርም፤ “በራቸውን ከፍተው እየተኙ፣ ሌባ ሌባ ይላሉ” የሚለውን አባባል ማስተዋል ወቅታዊ ነው፡፡ በሌላ ወገንም ድጋፍን ከልኩ በላይ አጋኖ ማሰብ፤ “አንገቷን ደግፈው ቢያስጨፍሯት፤ ያለች መሰላት” የተባለውን መዘዝ ያመጣል፡፡
ፈረንጆቹ There is no free lunch የሚሉት (ምንም ነገር በነፃ አይገኝም እንደማለት) የዋዛ ነገር አይደለም፡፡ የሚያስከፍለን ነገር መኖሩ ገሀድ ነው፡፡ ግን ቅናሹን ዋጋ ማስተዋል አለብን፡፡ ሁሉን በሚዛን መጫወት ከአጓጉል ቡጢ ያድናል፡፡ እኛን ከሌላ አፍሪካ አገራት ምን ይለየናል? ልዩ የሚያደርገን የኢኮኖሚ ጥሪት አለን ወይ? የፖለቲካ መረጋጋታችን አስተማማኝ ነወይ? እዚያው ሞላ እዚያው ፈላ (Volatile) የሆነው የምሥራቅ አፍሪካ አባዜ ምን ያህል አይመለከተንም? “ሠርጌን አሙቅልኝ” የሚባለው ዓይነት የፖለቲካ ዘፋኝ፤ ጠንቋይ፣ ከዶክተር አይለይም በሚልባት አፍሪካ፣ የተሟሟቀ ልማት አለኝ ማለት ይቻላልን? የአፍሪካ የመከላከያ ኃይል ምን ያህል የአፍሪካ ህብረት ታዛዥ ይሆናል? የድንበረተኛ አገሮች ፍቅርስ ወረት ነው ዘላቂ? ራሳቸውን ያላረጋጉ አገሮች እንደ አሜባ የከበቧት አገራችን፤ እንዳትዋጥ እንዳትሰለቀጥ መጠንቀቋ ዋና ጉዳይ ሆኖ ለሌሎች መጠቀሚያና ማነጣጠሪያ እንዳትሆን፣ መሬት የያዘ ዕሳቤ አላትን? ብሎ መጠየቅ ያባት  ነው ! ዙሪያችን ያሉትን ሁሉ በነቃ ዐይን፣ በዐይነ - ቁራኛ መመልከት፤ ያለ፣ የነበረ ወደፊትም የሚኖር፣ መላ ነው፡፡ አለበለዚያ፤ “የጨው ገደል ሲናድ፤ ብልጥ ያለቅሳል፣ ሞኝ ይልሳል” ይሆንብናል፡፡  

Published in ርዕሰ አንቀፅ

       ከአዘጋጁ፡-
በአውስትራሊያ የሚታተም “አሻራ” የተሰኘ መጽሔት በቁጥር 2 ዕትሙ፣ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማሪያምን በተለያዩ ጽሑፎች ዘክሯል፡፡ እኛ ግን ለዛሬ ልጃቸው ዶ/ር መቅደስ መስፍን ወልደማሪያም ከመጽሔቱ ጋር ያደረገችውን ቃለምልልስ መርጠን ከመለስተኛ የአርትኦት ሥራ በኋላ ለአንባቢያን አቅርበነዋል፡፡

         ዶ/ር መቅደስ መስፍን ወልደማሪያም ማን ናት?
               (የፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም ልጅ)

   ራስሽን ለአንባቢ በማስተዋወቅ ውይይታችንን ብትጀምሪልን?
ስሜ መቅደስ መስፍን ይባላል፡፡ የፕሮፌሰር መስፍን የመጀመሪያ ልጅ ነኝ፡፡ የምኖረውም አሜሪካን አገር ማሳቹቴስ ግዛት ነው፡፡ ወደ አሜሪካ ከመጣሁ ከ20 ዓመት በላይ ሆኖኛል፡፡
በኢትዮጵያ እያለሁ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን የተከታተልኩት በናዝሬት ትምህርት ቤት ሲሆን በከፍተኛ ትምህርት ደግሞ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የህክምና ፋክሊቲ ምሩቅ ነኝ፡፡ አሜሪካን ሃገር ከመጣሁ በኋላም በቦስተን ዩኒቨርሲቲ በ Public Health የማስተርስ ዲግሪ አግኝቻለሁ፡፡ በዚሁ ሙያ ከኢሚግራንቱ ጋር በተገናኘና በኤችአይቪ መከላከል (HIV Prevention) ለረዥም ጊዜ ሥሰራ ቆይቻለሁ። አሁን ደግሞ በግል አንዳንድ ስራ ለመጀመር እየተዘጋጀሁ ነው፡፡
በቅርቡ በአንድ አጋጣሚ “Eforall 2015 Finalists” በሚል ከተዘረዘሩት 18 ሰዎች ውስጥ ስምሽን አይቻለሁ። ለመሆኑ ይህ Eforall የተሰኘው ድርጅት ምን እየሰራ ያለ ድርጅት ነው? ያንቺ ስም በFinalist ዝርዝር ውስጥ የሰፈረው ምን ሰርተሸ ነው?
(Entrepreneurship for all) ወይም በአጭሩ (Eforall) የተሰኘው ድርጅት አነስተኛ የቢዝነስ ሃሳቦችን የሚያበረታታ መንግስታዊ ያልሆነ ተቋም ነው፡፡ ይህ ተቋም ሰዎች በራሳቸው ተነሳሽነት የቢዝነስ ሃሳብ አፍልቀው ወደ ተግባር ለመለወጥ የሚያደርጉትን ጥረት የሚያበረታታ ድርጅት ነው። አሰራሩም በመጀመሪያ ወደ ተግባር የሚለወጥ ቢዝነስ ሃሳብ አለን የሚሉ ሰዎችን ሃሳባቸውን ዘርዝረው በማመልከቻ መልክ ያቀርባሉ፡፡ ድርጅቱም የቀረቡለትን ማመልከቻዎች በተለያዩ መመዘኛዎች አወዳድሮ የበለጠ አሳማኝ ሆነው ያገኛቸውን ተቀብሎ ዕቅዳቸውን ወደ ተግባር የሚለውጡበትን መንገድ በተለያየ መልክ ያግዛል። እኔም እንዲሁ አንድ ያሰብኩትን ነገር ለመሞከር ጥናት እያደረኩ ባለሁበት ወቅት ነበር ድንገት ከዚህ ድርጅት የተደወለልኝ። ከዚህ በፊት ስለዚህ ድርጅት ምንም የማውቀው ነገር አልነበረም፡፡ ደውለው “እያደረግሽ ያለውን ሙከራ እያየን ነው። እኛ እንዲህ ዓይነቱን በግል ተነሳሽነት የሚደረጉ ጥረቶችን የምናበረታታ መንግስታዊ ያልሆንን ድርጅት ነን፡፡” ብለው ራሳቸውን ካስተዋወቁኝ በኋላ፤ ለምን ሃሳብሽን በዝርዝር ገልጸሽ ማመልከቻ አታስገቢም? በርግጥ ያመለከተ ሁሉ ላንቀበል እንችላለን፡፡ ውድድሩ ጠንካራ ነው፡፡ ግን መሞከርሽ አይከፋም” ብለው ምክር ሰጡኝ። እኔም ሃሳባቸውን ተቀብዬ እንደተባልኩት አደረግኩ። በኋላም ከ80 ያህል አመልካቾች መካከል አስራ ስምንታችንን ብቻ ተቀበሉን፡፡ እንዳሉትም ውድድሩ በጣም አስቸጋሪ ነበር። ማመልከቻ አስገብቶ መጠበቅ ብቻ ሳይሆን በየግዜው እየጠሩ ሃሳብክን በባለሙያ ፊት እንድታስረዳ ያደርጉሃል። ለሚቀርብልህ ጥያቄ ሁሉ አሳማኝ መልስ መስጠት አለብህ፡፡ ምክንያቱም እነሱን ካላሳመንክ ሌላውንም ማሳመን አትችልም ከሚል እምነት ነው፡፡ ትክክልም ይመስለኛል። አንዴ ከተቀበሉ ግን ራስህን ችለህ እስክትቆም ድረስ በሁሉም መልክ ያግዙሃል ይረዱሃል፡፡ ብዙ ልፋት ያለው ነገር ነበር። ሆኖም ግን ከ18 ተመራጮች መካከል ሆኜ ቀጣዩን ማለትም ወደ ተግባር የሚገባበትን ጎዳና ለመጀመር በዝግጅት ላይ ነኝ፡፡ Eforall 2015 Finalists ስም ዝርዝር ውስጥ ስሜ የተጠቀሰው በዚህ ምክንያት ነው፡፡ ከመነሻዬ በደፈናው በግል አንዳንድ ስራ ለመጀመር እየተዘጋጀሁ ነው ያልኩትም ይህንኑ ነበር፡፡
ወደ ፕ/ር መስፍን እንመለስ፤ ፕሮፌሰርን እንደ አባት እንዴት ትገልጫቸዋለሽ? አሁን ላለሽ ማንነት የሳቸው አስተዋፅኦ ምን ያህል ነው? ፕሮፌሰር በትምህርት ላይ ባላቸው ጠንካራ አቋም ይታወቃሉና በዚህ ረገድ በልጅነት ዘመን በጥሩም በመጥፎም የተከሰተ ትዝታም ካለ?
እንዳልከው በትምህርት ላይ ያለው አቋም ጠንካራ ነው፡፡ ያም ሊሆን ይችላል እኛም ብዙ አላስቸገርንም። የሚፈለገውን ውጤት ስለምናመጣ ብዙም በቁጣም ሆነ ውጤት ከማጣት ጋር በተያያዘ የማስታውሰው ነገር የለም፡፡ ከሱ ይልቅ ትዝ የሚለኝ በሃይስኩል እያለን የነበረበት የስራ ውጥረት ነው፡፡ ከስራ ወጥቶ ትምህርት ቤት መጥቶ ነው ወደ ቤት የሚወስደን፤ አንዳንዴ ግን ስለሚቆይብን ብቻችንን ትምህርት ቤት ውስጥ የመቆየት ነገር ነበር (ሳቅ)፡፡
ሌላስ እንደ አባት የሚገለጽ ባህሪ የላቸውም? ቁጡ! የሚፈሩ?
ብዙ ጊዜ ጓደኞቹ አባቴ ይቆጣል! አባቴን እፈራዋለሁ … ሲሉ ይገርመኝ ነበር፡፡ እኛ ጋ እንደዚህ አይነት ነገር የለም፡፡ ከአፉ አውጥቶ ካልተናገረ በስተቀር ምንም የምናውቀው ነገር አልነበረም። የሚነግረን ነገር ካለም ረጋ ብሎ ነው የሚነግረን። ግርፊያ፤ ዱላ፤ ቁጣ … የሚባል ነገር የለም፡፡ ጥፋት እንኳ ብታጠፋ ቁጭ አድርጎ የሚነግርህ ነገር ማጥፋትክን እንድትጠላው ነው የሚያደርግህ፡፡ እንዲህ አይነቱ አጋጣሚ ደግሞ ብዙም አልነበረም፡፡
ሌላው ልነግርህ የምፈልገው “ቅድሚያ ለእንስት” (Ladies First) በሚለው መርህ ላይ ያለውን እምነት ነው፡፡ እኔ ልጅም ሆኜ አሁን ጓደኞቼ አብዛኞቹ ወንዶች ናቸው፤ ብዙ ግዜ “ቅድሚያ ለእንስት” (Ladies First) በሚለው መርህ ላይ እንከራከራለን፤ ለምንድነው ቅድሚያ ለሴት የሚሰጠው ዓይነት ክርክር ማለቴ ነው፤ ይህ መርህ ግን ለአባባ አፋዊ ሳይሆን የውስጥ እምነቱ ነው፡፡ ለሴት ልጅ ክብር አለው፡፡
አንድ አጋጣሚ ልንገርህ፡- ወደ አሜሪካ ልመጣ ስል፤ ኢሚግሬሽን ለፓስፖርት ይሁን አሜሪካ ኤምባሲ ለቪዛ ይሁን አሁን ዘንግቼዋለሁ፤ ከሱ ጋር አብረን ሄደን ነበር። በቀኑ በጣም ብዙ ባለ ጉዳይ ስለነበር መቀመጫም አልተገኘም፡፡ በኋላ ቀደም ብለው መጥተው ወንበር አግኝተው ከተቀመጡት ሰዎች መካከል እሱን የሚያውቁ ሰዎች እንዲቀመጥ ተነሱለት፡፡ እሱ ደግሞ “አንቺ ተቀመጪ አለኝ”። እንዴ …? የተነሱት ላንተ ነው እኔ አልቀመጥም አልኩ፡፡ እሱ ግን “አንቺ ቆመሽ እኔ አልቀመጥም” ብሎ አስቀምጦኛል፡፡ ይህ የሚያሳየው ለሴት ልጅ ያለውን ክብር ነው፡፡
እኔና እህቴን አስቀምጦ ሲመክረን ብዙ ግዜ ሴት ልጅ ከጾታዋ ጋር በተያያዘ ሊደርስባት የሚችለውን ችግር ካስረዳን በኋላ መፍትሄው ደግሞ ትምህርት እንደሆነ አያይዞ ነበር የሚነግረን፡፡ በዚህ መልኩ ነበር የትምህርት ወሳኝነት ውስጣችን የሚያሰርፀው፡፡
ፕ/ር ብዙ የሚታወቁባቸው ጠንካራ የሰብዕና መገለጫዎችና ተያይዞም ችሎታዎች አሏቸው፡፡ ወዳንቺ የመጣው የትኛው ነው?
በልጅነቴም ብዙ ሰዎች በመልክ ትመስይዋለሽ ነው የሚሉት፡፡ ሌላ ሌላው ባብዛኛው ለሌላ ሰው የሚታይ ወይም ሌላው ሊናገረው የሚችል እንጂ ራስህ ስትናገረው ይከብዳል፡፡ ከሱ የተማርኩት የሚመስለኝ አንድ ነገር ፡- አልችለውም ብሎ ተስፋ መቁረጥ የሚባል ነገር የለብኝም። ማድረግ እችላለሁ (I can do it!) ብዬ ነው የምነሳው! የጀመርኩትን ግብ ሳላደርስ ተስፋ ቆርጦ ያለመቆም ዕልህ አለብኝ። ይህም ከሱ የመጣ ይመስለናል። እሱ በዚህ እድሜው እንኳ አንድ ነገር ከጀመረ ጫፍ ሳያደርስ ምንምና ማንም አያቆመውም፡፡
ሌላው ከሱ ወሰድኩ የምለው ጥቃትን በይሁንታ ወይም በያልፋል አይነት ትዕግስት አመለቀበልን ነው። አሁን ለምሳሌ እሱ የታሰረ ጊዜ እንደኔው ቤተሰባቸው ወይም አባታቸው የታሰሩባቸው ጓደኞቼ የሆነውን ተቀበሎ የማለፍን ነገር ሲያወሩ፣ ለኔ በፍጹም አይዋጥልኝም ነበር። የኔ ጥያቄ በመጀመሪያስ ለምን ይሆናል? ለምን ይታሰራል? ነው፤ አግባብ ያልሆነ ነገር ሲፈጸምብህ ወይም መብትህ ሲነካ ታግለህ መብትን ማስከበር እንጂ ስለ ምህረትና ስለ መሳሰሉት ነገሮች ማሰብ ትክክል አይመስለኝም፡፡ ይህም እምነቴ ከሱ የተገኘ ይመስለኛል፡፡
ከፕ/ር የምታደንቂላቸው ችሎታና ባህሪዎች ጥቂቱን ልትጠቅሺልኝ ትችያለሽ…?
በመጀመሪያ የተፈጥሮ ስጦታ በመሆኑ ክሬዲት የሚሰጠው ባይሆንም የሱ ጭንቅላት የተለየና በጣም የሚደንቅ ነው፡፡ በትንሽ ጊዜ ውስጥ አንድን ነገር ከተለያየ አቅጣጫ አይቶ ላንተ የማይታይህን ነገር አይቶ የሚያቀርብበት ችሎታው ሁሌም ያስገርመኛል። አንድ አወያይ ሃሳብ ከተነሳ ያ ሃሳብ ብትንትኑ ወጥቶ ካልቀረበ አይረካም፡፡ የሰው ሃሳብ በትዕግስት ያደምጣል። እሱም ያለመሰልቸት ያስረዳል፡፡ ባጠቃላይ ሃሳብን የመመርመር ችሎታና ትዕግስቱን አደንቃለሁ፡፡ ሌላው ደግሞ ያመነበትን ነገር ፊት ለፊት ከመናገር የሚያቆመው የለም።
አሁን ባለንበት ህብረተሰብ አንድን ሀሳብ ተቃውመህ አልያም ወጣ ያለና የተለየ ሃሳብ ይዘህ ስትቀርብ እንደ ጠላት ወይም እንደ ድፍረት የመውሰድ ነገር እየተለመደ ነው፡፡ የታየህን ነገር በግልጽ ስትናገር ሃሳብህን እንደተለየ ሃሳብ ተቀብሎ በዚያው ስሜት ከመመዘን ይልቅ ከጥላቻ እንደመነጨ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ እንዲህ ዓይነት ልምድ እየገዘፈ በሄደበት ህብረተሰብ ውስጥ እንደ አባባ አይነት ሃሳቡን በግልጽ የሚናገር ሰው ብዙ አስቸጋሪ ነገሮች ይገጥሙታል፡፡
በሦስት መንግስታት ውስጥ ሲያልፉ በተለያየ አጋጣሚ በትረ ስልጣኑን ከያዙት አካላት ጋር በነበራቸው አለመግባባት ቤተሰባችሁ ስጋት ውስጥ የወደቀበት የምታስታውሺው ትዝታ ካለ? በተለይ መንግስቱን ውረድ ባሉበት ወቅት ምን ተሰማሽ?
በመጀመሪያ የታሰረው እኔ ገና የ11 ወይም የ12 ዓመት ልጅ ሆኜ ይመስለኛል፡፡ የረብሻው ምክንያት በጊዜው ባይገባኝም አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተረበሸ ተብሎ እሱም ታስሮ ቤት ውስጥ የነበረው ግርግር ትዝ ይለኛል፡፡ ያኔ ደግሞ አዋቂ ሲያወራ ልጅ ወደ ውጭ ወይም ወደ ጓዳ የሚባልበት ዘመን ነበርና ስለታሰረበትና ስለረብሻው ምክንያት ብዙም የማስታውሰው ነገር ባይኖርም እንዲሁ ብቻ መታሰሩ ቤተሰቡን እንዳሳሰበ ትዝ ይለኛል፡፡
ሌላው እንዳልከው መንግሥቱ ኃይለማሪያምን ውረድ ባለበት ወቅት የተፈጠረው ነው፡፡ ያን ሁኔታ አሁንም ድረስ ሳስበው ይገርመኛል፡፡ በጊዜው እኔ እዚሁ አሜሪካን ሀገር ነበርኩ፡፡ ይህ በሆነበት ዕለት ወይም ማግስት ይመስለኛል አንድ ለሱም ለኔም ወዳጅ የሆነ ሰው ደውሎ “መስፍንን ሰሞኑን አግኝተሸዋል? “ሲል ጠየቀኝ፡፡ አይ ሰሞኑን አላገኘሁትም ብዬ ከመለስኩ በኋላ ነገሩ ስለከነከነኝ ምነው? ምን የተፈጠረ ነገር አለ? ብዬ ጠየቅኩት፡፡
“አይ አሁንም፣ በቃ መንግሥቱን ውረድ ብሎት አሁን ያለበት አይታወቅም፤ (He is in hiding)” አለኝ። በመጀመሪያ በጣም ደነገጥኩ፤ ተደብቋል የሚለው ነገር ከአባባ ተፈጥሮና ባህሪ ጋር በፍጹም የሚስማማ አልሆነልኝም፡፡ ልቀበለው አልፈለኩም፡፡
በመሆኑም ወዲያው ደውዬ ለማረጋገጥ ፈለኩ። ላገኘው አልቻልኩም፡፡ ይህ በእንዲህ እያለ ያው ወዳጃችን መልሶ ደውሎ “ተደብቋል ያልኩሽ ቀልዴን ነው፡፡ መንግሥቱን ግን ውረድ ብሎት መንግሥቱ ሳይበሰጫጭ አልቀረም” ከጉዳዩ ክብደት አንፃር ቀልዱ ባይገባኝም፣ ተደበቀ የሚለው ነገር እውነት አለመሆኑን መቀበል አልከበደኝም፡፡
በኋላም ደውዬ ሳገኘው ተረጋጋሁ፡፡ እንደተፈራው አልሆነም፤ መንግስቱም አገር ጥሎ ጠፋ፤ ሁሉም በዚሁ አበቃ፡፡ እንደሰማሁ ግን በጣም በጣም ነበር የደነገጥኩት።
የእሳቸው ልጅ በመሆንሽ ምን ይሰማሻል?
ይሄ ምን ያጠያይቃል ብለህ ነው? (ሳቅ) የሱ ልጅ በመሆኔ በጣም! በጣም ነው የምኮራው፡፡ በነገራችን ላይ እናቴም ያልተዘመረላት ጀግና እንደሚባሉት አይነት ነች። ከነዚህ ሰዎች መፈጠሬ ለኔ ክብሬም ኩራቴም ነው፡፡
እኔ ብቻ ሳልሆን ሁላችንም ኢትዮጵያዊያኖች እዚህ የደረስነው ብዙ ዋጋ ተከፍሎ ነው፡፡ ለሃገራቸው ድንቅ ስራ ሰርተው፤ ግዙፍ መስዋዕትነት ከፍለው ለዛሬው ማንነታችን ያበቁንን አባት እናቶቻችንን ውለታ ተሸክመን ነው የምንኖረው፡፡ እኔም ከሱ በመፈጠሬ ደስታዬ ወሰን የለውም፡፡

  የውሃ ሀብታችንን እንጠብቃለን - አርቲስት ችሮታው ከልካይ
                               
      የስምጥ ሸለቆ ሐይቆች ተፋሰስ ባለሥልጣን ከግሪን ኢንሼቲቭ ኢትዮጵያ ዴቨሎፕመንት አሶሴሽን ጋር በመተባበር በተፋሰሱ የሚገኙትን ሐይቆች ከጉዳት ለመከላከል “ሐይቆቻችንን መጠበቅ የቀን ተቀን ሕይወታችን ሲሆን ይገባል” በሚል መርህ ለተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ግንዛቤ ለማስጨበጥ የንቅናቄ ፕሮግራም ጀምሯል፡፡ ከንቅናቄ ፕሮግራም ዘዴዎች አንዱ አርቲስቶች ሐይቆቹ ያሉባቸውን ችገሮች ተረድተው በሙያቸው ኅብረተሰቡን እንዲያስተምሩና ግንዛቤ እንዲያስጨብጡ ማድረግ ነው፡፡
በዚሁ መሠረት ከትናንት በስቲያ በሀርመኒ ሆቴል ለግማሽ ቀን በተዘጋጀ ፕሮግራም አርቲስቶቹን በመጋበዝ የስምጥ ሸለቆ ሐይቆች አሁን ያለባቸውን ችግር፣ ወደፊት ሊደርስ ይችላል ተብሎ የተፈራውን ስጋት አሳውቋል፡፡ አርቲስቶቹ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርቱን ከተከታተሉ በኋላ “ውሃ ሕይወት ነው” የሚለውንና ከልጅነታቸው ጀምሮ የሚያውቁትን አባባል በዕለቱ በተደረገላቸው ገለፃ ከአባባልነት ባለፈ ውሃ በእርግጥም ሕይወት መሆኑን፣ እንስሳትም ሆኑ ዕፅዋት ያለውሃ ሕልውና እንደሌላቸው መገንዘባቸውን ተናግረዋል፡፡
እስከዛሬ ድረስ ስለሐይቆች ያለን ግንዛቤ መዝናኛነታቸው ነበር፡፡ በዛሬው ትምህርት ስለውሃ ብዙ ተገንዝበናል፡፡ ውሃ ሕይወት ነው ከሚለው የዘለለ ግንዛቤ አልነበረኝም ያለው አርቲስት ችሮታው ከልካይ ውሃ ለፍጡራን ሁሉ ያለውን ጥቅም፣ በሕይወት መኖርም ሆነ ዕድገት ከውሃ ውጭ በጭራሽ እንደማይታሰብ መገንዘቡን ተናግሯል፡፡ ውሃን ብንጠብቅ ሕልውናችን እንደሚጠበቅ ተረድተናል፡፡ ውሃ ስንል ለአንደበታችን ቀላል ይመስላል። ውሃ ዓለም አቀፋዊ ነው፡፡ ሰዎች ለመኖር፣ ዕፅዋት ለማደግ፣ ገበሬው ለእኛ ለሚያቀርበው ምርት፣ ለሚያረባቸው እንስሳት፣ … ውሃ እንደሚያስፈልጋቸው፣ ጠቀሜታው ከፍተኛ መሆኑን፣ ነገር ግን ለውሃ ትኩረት ባመስጠታችን የሚደርሰውን ጉዳት ተረድተናል ብሏል፡፡
ማንኛውም ሰው ውሃ እንዳያልቅ በአግባብ መጠቀም፣ እንዳይቆሽሽና እንዳይበከል ቆሻሻን በጥንቃቄና በተገቢው መንገድ ማስወገድ እንዳለበት ተረድቻለሁ ያለው አርቲስቱ፡፡
የውሃ መቀነስና መበከል ለትውልድ የሚተላለፈ ከፍተኛ ችግር እንደሚያስከትል ተረድተናል፡፡ ስለዚህ ኅብረተሰቡ ውስጥ ገብቶ ማስተማርና መቀስቀስ ያስፈልጋል፡፡
እየተወንም ሆነ እየዘመርን፣ እያሳቅንም ሆነ እየገጠምን ውሃን እንጠብቃለን በማለት ገልጿል፡፡
የሐይቆች የመጥፋት አደጋ በሐሮማያ ላይ ብቻ የተከሰተ አለመሆኑን የገለፀው የቲያትር ደራሲው ውድነህ ክፍሌ ሌሎች ሐይቆችም ይኸው ጥፋት እንዳንዣበበባቸውና ትግራይ ውስጥም የጠፋ ሐይቅ መኖሩን ተናግሯል፡፡ ውሃው (ሐይቁ) የነበረበትን ዙሪያ ገበሬዎች እያረሱ ነው፡፡ አደጋ ከፊታችን ተደቅኗል ማለት ነው፡፡ በዓይናችን እያየን ያለው የገጸ ምድር ውሃ እየጠፋ ነው፡፡ ስለዚህ በአጠቃላይ ከአርቲስቶች ብዙ ይጠበቃል።
የፕሮግራሙ
አዘጋጆች እኛን ያስተማሩትና ያሳወቁን ኅብረተሰቡ ውስጥ ገብተን በሚረዳው ቀላል መንገድ ግንዛቤውን ከፍ እንድናደርግ ነው ያለው ደራሲ ውድነህ ክፍሌ ወደ ሐይቆቹ እየሄድን የተደቀነባቸው አደጋ የፈጠረብንን ውስጣዊ ስሜት በመግለጽ ውጤታማ የግንዛቤና ቅስቀሳ እንደምናደርግ እርግጠኛ ነኝ ብሏል፡፡  
አርቲስት አስቴር ዓለማየሁ በበኩላ፣ የሀሮማያ ሐይቅ መድረቅ በቴሌቭዥን ሲተላለፍ አይቼ በጣም አዝኜ ነበር። አሁን በተሰጠን ትምህርት ሌሎች ሀይቆችም ተመሳሳይ ዕጣ እየጠበቃቸው መሆኑን ተረድቻለሁ፡፡ እንደዜጋና እንደሙያተኛ ኃላፊነት እንዳለብኝ ተስምቶኛል፡፡ ህዘቡ ይወደናል፣ ያከብረናል፡፡ ህዝቡ የሰጠንን የፍቅር ሀብት በመጠቀም ህብረተሰቡ ውስጥ ገብቼ በመቀስቀስና በማስተማር የዜግነት ድርሻዬን ለመወጣት ተነስቻለሁ በማለት ስሜቷን ገልጻለች፡፡
የስምጥ ሸለቆ ሐይቆች ተፋሰስ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክር ዶ/ር ከበደ ካንቹላ ውሃ በህይወት ለመኖር አስፈላጊ ከመሆኑም በላይ ለዕድገትም አስፈላጊ መሆኑን ሲገልጹ፤ … የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር፣ የቤቶች ግንባታ፣ ታላቁ የህዳሴ ግድብ፣ … ማንኛውም ግንባታ የሚሰራው ሲሚንቶና ውሃ ሲደባለቅ ነው፡፡ ዳንጎቴ፣ ሙገር፣ ደርባ፣ መሰቦ፣ … የፈለገው ዓይነት ሲሚንቶ ቢሆን ያለ ውሃ አንዳች የሚፈይደው ነገር የለም፡፡ ሲሚንቶ‘ኮ የተቃጠለ  አመድ ነው ያሉት በማለት አስረድተዋል፡፡
ዶ/ር ከበደ ስለውሃ ጠቀሜታ በስፋት ካስረዱ በኋላ ሐይቆቹ የሚሰጡትን አገልግሎት እንዳይቀጥሉ የሚያደርግ አደጋ እንደተጋረጠባቸው ጠቅሰው፤ አደጋዎቹም የሐይቆች መበከልና የውሃ መቀነስ እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡ ለምሳሌ “የፍቅር ሐይቅ” የሚባለው የሀዋሳ ሀይቅ፣ ፍቅረኛሞች ሲዝናኑ ለመጠጣት ይዘው የሄዱትን ውሃ ሲጨርሱ የውሃውን መያዣ ፕላስቲክ ሐይቁ ውስጥ ስለሚጥሉና በሌሎችም ቆሻሻዎች መበከሉን፣ የዝዋይ ሐይቅ ደግሞ በመሬት መራቆት የተነሳ ደለል ስለሚገባበት እንዲሁም በምዕራብ ጎኑ ብቻ በ6 ሺ ፓምፖች ለመስኖ ውሃ ስለሚሳብ ውሃው እየቀነሰ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ባለሥልጣኑ በያዝነው በጀት ዓመት (2008) በዝዋይ - ሻላ፣ ሀዋሳ፣ አባያ - ጫሞ ሐይቆች በዘላቂና የተቀናጀ የውሃ አስተዳደር ከብክለትና ከደለል ሙላት ለመከላከል ፕሮጀክት ቀርፀውና ለመንግሥት አቅርበው ከመደበኛ በጀት ሌላ 24 ሚሊዮን ብር እንደተፈቀደላቸው ተናግረዋል፡፡
ለእያንዳንዱ ሐይቅ ከአርቲስቶች አምባሳደር ይሾማሉ ያሉት ደግሞ የግሪን ኢንሼቲቭ ኢትዮጵያ ዴቨሎፕመንት አሶሴሽን መስራችና ዋና ዳይሬክተር አቶ ፋሲል አስማማው፣ በየቴአትር ቤቶቹ ግንዛቤ እንዲፈጠር ሐይቆቹን እንደሚያከፋፍሉ፣ ከህብረተሰቡ ጋር የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ እንደሚሰሩ፣ … ገልጸዋል፡፡

Published in ጥበብ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በኢትዮጵያ ያደረጉትን ጉብኝት አስመልክቶ የተለያዩ አስተያየቶች እየተሰነዘሩ ሲሆን ተቃዋሚዎች ፕሬዚዳንቱ በጉብኝታቸው የኢትዮጵያን የሰብዓዊ መብት አያያዝና የዲሞክራሲ ሁኔታ ትኩረት ነፍገውታል ብለዋል፡፡ ኦባማ፤ የኢትዮጵያ መንግሥት “በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ ነው” ማለታቸውን ተቃዋሚዎች ተቃውመውታል፡፡
መንግሥት በበኩሉ፤ ፕሬዚዳንት ኦባማ እውነታውን ነው የገለፁት ብሏል፡፡  
የፕሬዚዳንቱን ጉብኝት አስመልክቶ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች የሚሰነዝሯቸው ትችቶች ውሃ የማይቋጥሩ ናቸው ሲልም መንግሥት ነቅፏል፡፡
በማህበራዊ ድረገፆች ላይ የግል ፖለቲካዊ ዕይታዎቹን በማቅረብ የሚታወቀው የፖለቲካል ሣይንስ ተመራቂው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በሰጠው አስተያየት፤ ኦባማ በኢትዮጵያ ጉብኝታቸው ያስተላለፉት መልዕክት ከጠበቀው በተቃራኒ እንደሆነበት ይናገራል፡፡
የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤትን ጨምሮ የተለያዩ ተቋማት ስለ ኢትዮጵያ ዲሞክራሲና የሰብአዊ መብት አያያዝ አሉታዊ ሪፖርቶችን እያወጡ ባሉበት ሁኔታ፣ ፕሬዚዳንቱ እዚህ ድረስ መጥተው “በአገሪቱ ያለው መንግሥት በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ ነው” በማለት እውቅና መስጠታቸው ፈፅሞ ያልጠበቅሁት ነው” ብሏል፡፡ በፕሬስ ነፃነት ጉዳይና በሰብአዊ መብት አጠባበቅ ላይ ፕሬዚዳንቱ ይፈጥራሉ ብዬ የጠበኩትን ያህል ተፅዕኖ አለመፍጠራቸውን ተገንዝቤአለሁ ብሏል፡፡
ፕሬዚዳንቱ በአፍሪካ ህብረት ያደረጉት ንግግር ይበልጥ ቴክኒካል የሆነ ዲፕሎማሲያዊ ንግግር ነው ያለው ጋዜጠኛው፤ “ያ ግን በአጠቃላይ አፍሪካን እንጂ ኢትዮጵያን የሚመለከት ባለመሆኑ የሀገሪቱን የመንግስት እንቅስቃሴ ለሚከታተል ኢትዮጵያዊ ትርጉም አልባ ይሆንበታል” ብሏል፡፡
እንደ አጠቃላይ ዲፕሎማሲያዊ ንግግር ከተወሰደ ፕሬዚዳንቱ በአፍሪካ ህብረት ያደረጉት ንግግር ከሊበራል መሪ የሚጠበቅ ነው የሚለው አስተያየት ሰጪው፤ ፕሬዚዳንቱ እንዲህ ያለ ንግግር ሊያደርጉ የቻሉትም አሜሪካውያን ካላቸው ግብረ-መልስን እንደትልቅ ግብአት የመጠቀም የሠለጠነ አካሄድ በመነሳት፣ በቤተመንግስት በተሰጠው መግለጫ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ እንደተከፋ ተገንዝበው ያደረጉት የተሠላ ንግግር ይመስለኛል ብሏል፡፡
“ፕሬዚዳንቱ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ያላቸውን ትክክለኛ አቋም ያንፀባረቁት በቤተመንግስት በሠጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ነው፤ በአፍሪካ ህብረት ያደረጉት ንግግር የሽንገላ ነው” ሲልም ትዝብቱን ገልጿል፡፡
“ባለፈው እሁድ አመሻሽ ላይ ፕሬዚዳንት ኦባማ ወደ ኢትዮጵያ ሲገቡ ስመለከት ከደስታዬ ብዛት አልቅሻለሁ” ያለው ሌላው አስተያየት ሰጪ በባህርዳር ዩኒቨርሲቲ የሁለተኛ ዓመት የጋዜጠኝነት ተማሪ የሆነው ቢንያም በበኩሉ፤ ፕሬዚዳንቱ በሃገሪቱ ያለውን ለውጥ መመልከታቸውና ሰላም መሆኑን ማየታቸው ትልቅ ነገር ነው ባይ ነው፡፡
“ፕሬዚዳንቱ እንዴት ኢህአዴግ በስልጣን ላይ እያለ ኢትዮጵያን ይጎበኛሉ? በሚለው ሃሳብ አልስማማም” ያለው ቢኒያም፤ “ማንም በስልጣን ላይ ቢኖር የታላቅ ሃገር መሪ መጥቶ ሲጎበኝ አገሪቱ ተሰሚነቷና ተቀባይነቷ እያደገ መምጣቱን ጠቋሚ ነው፤ ነገ ይሄ መንግስት ወርዶ በሌላ ቢተካም ሃገራዊ ጥቅምን አስቀድሞ ማየት ተገቢ ነው” ብሏል፡፡
ከጥቂት ዓመታተ በፊት ፕሬዚዳንት ኦባማ፤ ሆስኒ ሙባረክ የሚመሩትን ሃገር ለመጎብኘት ግብፅ መሄዳቸውን ያስታወሰው አስተያየት ሰጪው፤ በወቅቱ በኢትዮጵያ እንዳደረጉት ለ30 ዓመት በስልጣን ላይ ከቆዩት ሙባረክ ጋር ተወያይተው፣ ግብፅን አድንቀውና አንቆለጳጵሰው ተመልሰዋል፤ በጥቂት ወራት ውስጥ ግን የተፈጠረው ሌላ ታሪክ ነው፡፡” ይላል፡፡ በፕሬዚዳንት ኦባማ የተጎበኙት ሙባረክ፤ በህዝባዊ አመፅ ከስልጣናቸው ሲወርዱ አመፁን ከደገፉትና በአመፅ ስልጣን ላይ ለወጣው መንግሥት እውቅና ከሰጡት ቀዳሚ ሃገራት አንዷ አሜሪካ ነበረች በማለት አሁኑ ጉብኝት ዋስትና እንደማይሆን ገልጿል፡፡
“የኢትዮጵያ መንግስትም ቢሆን ሙሉ ለሙሉ በአሜሪካ የሚተማመን መንግሥት አይመስለኝም” ያለው አስተያየት ሰጪው፤ ፕሬዚዳንቱ በአፍሪካ ህብረትም ሆነ በብሄራዊ ቤተ መንግሥት ያደረጓቸው ንግግሮችና የሰጧቸው መግለጫዎች ብዙም የአቋም ለውጥ የሚያስከትሉበት አይመስለኝም” ብሏል፡፡
ፕሬዚዳንት ኦባማ በአፍሪካ ህብረት ባደረጉት ንግግር ላይ የተገኙት የኢዴፓ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደ በበኩላቸው፤ “የፕሬዚዳንቱን ንግግር ልብ ብሎ ያዳመጠ ሰው ጠንከር ያለ መልዕክት መያዙን ይረዳል” ይላሉ - በተለይ በዲሞክራሲ ሂደት ላይ የአፍሪካ መሪዎች መከተል የሚገባቸውን መናገራቸውን በመግለፅ፡፡ ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ መንግሥት የፕሬዚዳንቱን ንግግር ሰምቶ ተግባራዊ ያደርጋል የሚል ግምት የለኝም፤ ዶ/ር ጫኔ፡፡
ኦባማ፤ “በኢትዮጵያ በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ መንግሥት ነው ያለው” ማለታቸው ከዲፕሎማሲ ቋንቋነት የዘለለ ትርጉም አይኖረውም ያሉት የኢዴፓ መሪ፤ ኦባማ ሃገሪቱን ለመጎብኘት ሲመጡ የግድ በስልጣን ላይ ያለውን መንግስት መቀበል ስላለባቸው እንጂ ሙሉ እውቅና ከመስጠት ጋር አይያያዝም ባይ ናቸው፡፡
“በየትኛውም መንገድ አምባገነን መሪ በስልጣን ላይ ሊቀጥል ይችላል” የሚሉት የፓርቲው መሪ፤ ኃያላኑ መንግስታት ማተኮር የሚፈልጉት የዲሞክራቲክ ተቋማት በሚጠናከሩበት ሁኔታ እንደሆነም ያስረዳሉ፡፡
ልማት ያለ ዲሞክራሲ ብዙ አያስኬድም ያሉት ዶ/ር ጫኔ፤ የአረብ ሃገራት በልማት የመጠቁ ሃብታሞች ቢሆኑም በዲሞክራሲ ያለመጠናከራቸው በፈጠረባቸው ጣጣ  እንደገና እየፈረሱና እየወደቁ መሆናቸውን ጠቁመው፣ በኢትዮጵያም መልካም አስተዳደርና የህዝብ ይሁንታ ያለው መንግስት በስልጣን ላይ እስካልተቀመጠ ድረስ እድገቱ ቀጣይነት አይኖረውም ብለዋል፡፡ የኦባማ ንግግሮች ተፅዕኖ የመፍጠር አቅም አላቸው ብዬ አላስብም ያሉት ዶ/ር ጫኔ፤ የኢትዮጵያ መንግስት ካለው አደረጃጀትና አወቃቀር አንፃር እንዲህ በቶሎ ይቀየራል የሚል እምነት እንደሌላቸው ገልፀዋል፡፡
ባራክ ኦባማ ወደ ኢትዮጵያ መምጣታቸውን በበጎ ጎኑ እንደሚመለከቱት የተናገሩት ታዋቂው  ፖለቲከኛ አቶ ልደቱ አያሌው በበኩላቸው፤ ፕሬዚዳንቱ በሃገሪቱ በነበራቸው ቆይታ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ለውጦች መኖራቸውን መገንዘባቸው መልካም እንደሆነ ጠቁመው በሰብአዊ መብትና ዲሞክራሲ ጉዳይ ላይ ግን የነበራቸው ግንዛቤ የተዛባ ይመስለኛል ብለዋል፡፡ በንግግራቸው ላይ የመለሳለስና ከእውነታው የመሸሽ ነገር ማስተዋላቸውን በመግለፅ፡፡
ፕሬዚዳንቱ በጉብኝታቸው በኢትዮጵያ መንግስት ላይ የሚያውቁትን ያህል ትችት ይሰነዝራሉ ብሎ መጠበቅ ያስቸግራል ያሉት አቶ ልደቱ፤ የጉብኝታቸው አላማ የሁለቱን ሃገራት ግንኙነት ወደ ተሻለ ደረጃ ማድረስ በመሆኑ በአዎንታዊ ነገሮች ላይ ለማተኮር መርጠዋል፡፡ መጀመሪያም በመሬት ላይ ያለውን ሃቅ በትክክል የሚያሳይ ንግግር ያደርጋሉ ብዬ አልጠበቅሁም፤ የሆነውም እንደጠበቅሁት ነው ብለዋል፡፡
በአፍሪካ ህብረት ባቀረቡት ንግግር፣ የአፍሪካ መሪዎችን ስልጣንን የሙጥኝ ማለት በተመለከተ በቀልድ አዋዝተው ያስተላለፉት መልዕክት የተሻለ ነበር ያሉት አቶ ልደቱ፤ በኢትዮጵያ ያለውን የሰብአዊ መብት አያያዝና የዲሞክራሲ ሁኔታ ግን ያወቁ አልመሰለኝም፡፡ የሚያውቁትም ከሆነ ጠንከር ባለ ቋንቋ ለመግለፅ ድፍረት አጥተዋልሰ ብለዋል፡፡
የፖለቲካ ሳይንስ ምሁሩና የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር ዶ/ር መረራ ጉዲና በበኩላቸው፤ ፕሬዚዳንቱ በኢትዮጵያ ያለው መንግስት “በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ ነው” ማለታቸው ተገቢ አለመሆኑን ጠቅሰው በአፍሪካ ህብረት ባደረጉት ንግግር ግን መሰረታዊ ችግሮችን በማንሳት መናገር የሚገባቸውን ያህል ተናግረዋል ብለዋል። ከኢትዮጵያ ጋር የሚያስተሳስራቸው ዋነኛ ጉዳይ ሽብርተኝነትን የመዋጋት አጀንዳ ነው ያሉት ምሁሩ፤ በዲሞክራሲና በሰብአዊ መብት ዙሪያ ብዙም ተፅዕኖ ለማድረግ አለማሰባቸውም መነሻው ይሄው ነው ብለዋል፡፡
ሌላው አንጋፋ ፖለቲከኛና የመድረክ ሊቀመንበር ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ ደግሞ የፕሬዚዳንቱ ጉብኝት ለኢህአዴግ መንግስት ውዳሴና ቡራኬ ከመስጠት ባሻገር ብዙም ፋይዳ አልነበረውም ባይ ናቸው። “በጉብኝቱ ኢህአዴግ ድል ተቀዳጅቷል” ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ኦባማ የኢትዮጵያ መንግሥት “በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ ነው” ማለታቸውን የጠቀሱት ፕ/ር በየነ፤ ኢህአዴግ ከዚህ በላይ የሚፈልገው ነገር ሊኖር አይችልም ሲሉ ጉብኝቱ ለመንግሥት ትልቅ ድል ማስገኘቱን ገልፀዋል፡፡ ለእኛና ለህዝቡ ግን ምንም ፋይዳ አልነበረውም ይላሉ ፕ/ር በየነ፡፡
የኢህአዴግ ጽ/ቤት የህዝብና የውጪ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ደስታ ተስፋው ግን ከአብዛኛው አስተያየት ሰጪዎች የተለየ አቋም ነው ያላቸው። ኦባማ የኢትዮጵያ መንግሥትን “በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ ነው” ማለታቸው ትክክለኛ አቋም መሆኑን ጠቁመው፤ ይሄ ደግሞ የእሳቸው ብቻ ሳይሆን የአሜሪካ መንግሥትም አቋም ነው ብለዋል፡፡
“ተቃዋሚዎች አሁንም ምርጫውን በተመለከተ ራሳቸውን ዞር ብለው ማየት አለባቸው፤ ህዝቡ ኢህአዴግን ለምን መረጠ? እኛ ለምን ተሸነፍን? ችግራችን ምንድን ነው? የሚለውን በዝርዝር ማየት ይገባቸው ነበር፤ ነገር ግን ይሄን ለማድረግ አሁንም ፍላጎቱ የላቸውም” ያሉት አቶ ደስታ፤ ተቃዋሚዎች ከኢህአዴግም አልፈው የአሜሪካ መንግስትን በመወንጀል ላይ ናቸው ብለዋል፡፡ “ይሄ አካሄዳቸው ግን ትክክል አይደለም፤ ከእውነታው ያፈነገጠ ነው፤ የህዝቡን ውሳኔም ማክበር አለባቸው” ሲሉም አቶ ደስታ ተናግረዋል፡፡
የፕሬዚዳንቱ ጉብኝት በሰላም፣ በልማትና በዲሞክራሲ ዘርፎች የተቀዳጀነው ስኬት ውጤት ነው ያሉት አቶ ደስታ፤ ኦባማ አገሪቱ በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ መንግስት ያላት መሆኑን መመስከራቸው የአገሪቱን ገፅታ በበጎ መልኩ እንደሚገነባ ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

በአዲስ አበባ የሚንቀሳቀሱ ተሽከርካሪዎችን ለቅጣት በሚል ታርጋ መፍታት መከልከሉን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
መንጃ ፍቃድ ሳይዙ ማሽከርከር፣ የክስ ወረቀት ለ48 ሰዓታት ሳይከፍሉ ማቆየት፣ በማይፈቀድ የመንጃ ፍቃድ ደረጃ ማሽከርከር እንዲሁም የሚያጠራጥር መንጃ ፍቃድ ተይዞ ሲገኝ ትራፊክ ፖሊስን ጨምሮ ሌሎች የህግ አካላት ታርጋ ይፈቱ እንደነበር የጠቆሙት የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ ምክትል ኢንስፔክተር አሰፋ መዝገቡ፤ ይህ አሰራር አንዳንድ ህገ-ወጥ ግለሰቦች ሰሌዳውን ራሳቸው በመፍታት የተለያዩ ወንጀሎች እንዲፈፅሙ መንገድ በመክፈቱ የተሽከርካሪዎችን ታርጋ መፍታት ተከልክሏል ብለዋል፡፡ አሽከርካሪዎች የህግ ጥሰት ፈጽመው ሲገኙ ታርጋ ከመፍታት ይልቅ መኪናውን በቀጥታ ወደ ጣቢያ በመውሰድ ቅጣቱን እንዲያገኝ ይደረጋል ብለዋል - ምክትል ኢንስፔክተሩ፡፡ ታርጋ ሊፈታ የሚችልበትን ብቸኛ ምክንያት ሲጠቅሱም፤ የተከለከለ ቦታ መኪና ቆሞ ሲገኝና አሽከርካሪው ከሌለ ብቻ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡
አሽከርካሪው መኪናውን ከማንቀሳቀሱ በፊት የክስ ወረቀት ተቀብሎ ታርጋውን ሊያስመልስ እንደሚገባ የገለፁት ምክትል ኢንስፔክተሩ፤ ያለ ታርጋ ማንቀሳቀስ በፍፁም የተከለከለ ነው ብለዋል፡፡
ያለ ሰሌዳ በመኪና መንቀሳቀስ ወንጀል በመሆኑ ህብረተሰቡ በስልክ ቁጥር 011 1 11 01 11 በመደወል ለፖሊስ ጥቆማ እንዲያደርግ ወይም በአቅራቢያው ላለ ትራፊክ ፖሊስ እንዲጠቁም ኢንስፔክተሩ አሳስበዋል፡፡ ይህንን ህግ የማይተገብሩ ትራፊክ ፖሊሶች ከተገኙም አሽከርካሪዎች በዚሁ ስልክ ቁጥር እንዲያሳውቁ ጠይቀዋል፡፡
አዲሱ ህግ እየተሰራበት ያለው በመዲናዋ ብቻ መሆኑን በመግለፅም ህጉ በክልል ከተሞችም ቢተገበር ህገ ወጦችን ለመከላከል እንደሚያስችል ምክትል ኢንስፔክተር አሰፋ መዝገቡ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

አስከሬኑ ከትላንት በስቲያ ወደ አገሩ ተሸኝቷል
                              
    ላለፉት 33 ዓመታት በኢትዮጵያ የኖረው ሕንዳዊው መምህርና የሕፃናት መጽሐፍት ደራሲ ጆሴፍ ፍራንሲስ፣ ባለፈው ማክሰኞ ማታ መኖሪያ ቤቱ በር ላይ ወድቆ ሕይወቱ አለፈ፡፡ አስከሬኑ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ወደ ትውልድ አገሩ ህንድ በክብር ተሸኝቷል፡፡
በ1974 ዓ.ም በ29 ዓመቱ ከተወለደበት ደቡብ ሕንድ ታሚላዱ ማዱሬ ክልል፣ በመምህርነት ሙያ ወደ ኢትዮጵያ የመጣው ጆሴፍ ፍራንሲስ፤ የዕድሜውን ግማሽ ኢትዮጵያ ውስጥ በማስተማርና የሕፃናት መጻሕፍትን በመጻፍ ነው ያሳለፈው፡፡
በትምህርት ሚኒስቴር ተመድቦ በወሎ ሓይቅ ማስተማር የጀመረው ጆሴፍ፤ በመቀጠልም በአዲስ አበባ በቦሌ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት በእንግሊዝኛ መምህርነት አገልግሏል፡፡ ለበርካታ ዓመታትም በግሪክ የማኅበረሰብ ት/ቤት የእንግሊዝኛ ቋንቋና ማኅበራዊ ሳይንስ ሲያስተምር ቆይቷል፡፡
ለኢትዮጵያ ታሪክ ልዩ ፍቅር እንደነበረው የሚነገርለት ሕንዳዊው መምህር፣ “የዐድዋ ጦርነት”፤ “ዐፄ ቴዎድሮስ”፤ “ዓለማየሁ ቴዎድሮስ - የኢትዮጵያ ልዑል”፤ “ድንቂቱ ኢትዮጵያ” የተሰኙ መጻሕፍትን አሳትሟል፡፡  የኢትዮጵያ ሕፃናት የአገራቸውን ታሪክ እንዲያውቁ የሚያግዝ በአቅማቸው የተዘጋጁ የታሪክ መፃሕፍት አለመኖሩን የተገነዘበው ጆሴፍ ፍራንሲስ፣ የመጀመሪያ የህፃናት መጽሐፉን “The Battle of Adowa - የዐድዋ ጦርነት” በሚል ካሳተመ በኋላ ከሦስት የማያንሱ የታሪክ መጻሕፍትን ለህፃናት አዘጋጅቷል፡፡
የመጨረሻ መጽሐፉ ደግሞ “የድንቂቱ ኢትዮጵያ ድንቃ ድንቆች” (This is Ethiopia፡ A book of Fascinating Facts) የተሰኘ ሲሆን በኢትዮጵያ ሊጎበኙ የሚገባቸውን ድንቅ ቦታዎች በመዘርዘር የሚያስተዋውቅ ነው፡፡ ጆሴፍ ሌላ አዲስ መጽሐፍ በማዘጋጀት ላይ እንደነበር ታውቋል፡፡
በኢትዮጵያ ፍቅር ተማርኮ እዚሁ የቀረው ጆሴፍ፤ ባለፈው ማክሰኞ በ62 ዓመቱ ኦሎምፒያ አደባባይ ከሚገኘው የአፓርትመንት ቤቱ በረንዳ ላይ ላፕቶፑን እንዳነገተና መነጽሩን እንደያዘ መሬት ላይ ወድቆ ሞቶ ተገኝቷል፡፡
ከቅርብ ወዳጆቹ አንዱ የሆነው ጋዜጠኛ ጌጡ ተመስገን፣ ስለ ጆሴፍ ሲናገር፤ “እኔ የኢትዮጵያ ልጅ ነኝ፤ ለሕንድ አልሠራሁም፤ ስለዚህም ሕንድ እኔን አታውቀኝም፤ ስሞት ወሎ ሐይቅ ወስዳችሁ እንድትቀብሩኝ!” ብሎ በዚያች በምትናፍቀው ሣቁ ንግግሩን ያጅባታል፤ ዛሬም ያቺን ሣቁን እናፍቃታለሁ፡፡ የመጨረሻ ሣቁንና የማይጠገብ ጨዋታውን ከመሞቱ ሁለት ቀናት በፊት ቦሌ በምትገኝ ግሮሰሪ ውስጥ ነበር የሰማሁት፤ የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘጋቢ መለስካቸው አምሃና ሌሎችም ታላላቅ እንግዶች ነበሩ፡፡ ለካ ጆሴፍ እየተሰናበተን ነበር፤ እየተለየን፤ አላወቅንም እንጂ፤” ሲል ጌጡ ከሕንዳዊው ጓደኛው ጋር ያሳለፈውን የመጨረሻ ቀን አስታውሷል፡፡
ጆሴፍ፤ ከ11 ዓመታት በፊት የመጀመሪያ መጽሐፉ “የዐድዋ ጦርነት” መውጣቱን ተከትሎ ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር ባደረገው ቃለ - ምልልስ፤ ለታሪካዊ ቦታዎች ትልቅ ፍቅር እንዳለውና መጓዝ እንደሚወድም ገልፆ ነበር፡፡ በርግጥም ጆሴፍ ያልጐበኘው ታሪካዊ ስፍራ እንደሌለ የቅርብ ወዳጆቹ ይመሰክራሉ፡፡ የበርካታ የጥበብ ባለሞያዎች እና የጋዜጠኞች ባልንጀራ የነበረው ጆሴፍ፤ ድንገተኛ አሟሟቱ ለብዙዎቹ አስደንጋጭ ሆኖባቸዋል፡፡

Published in ዜና

  የሰንበት ት/ቤቶቹ እንቅስቃሴያቸውን አጠናክረው እን
                         ‹‹መልካም ዜጋ የምታወጣው ተቋም በሙስና መጎዳቷ ለሀገርም ጉዳት ነው”፤ ወንጀሉ ላይ መንግሥት መዋቅሩን                         ጠብቆ ይገባል፤ በሃይማኖቱ መሸፈን አይችሉም››        ዶ/ር ሺፈራው ተክለ ማርያም


        ከመልካም አስተዳደር ዕጦት እና ከተጠያቂነት ሥርዐት መጥፋት ጋር በተያያዘ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ መዋቅር ውስጥ ሰፍኗል በተባለው ምዝበራ እና ሙስና  መንግሥት መዋቅሩን ጠብቆ ሕጋዊ ርምጃ እንደሚወስድ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ከትላንት በስቲያ ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት አመራሮች ጋር በተካሔደው ውይይት፣ መንግሥት ከሃይማኖት ተቋማት ጋር በሰላም እና በልማት ጉዳዮች ላይ አብሮ እንደሚሠራ የጠቀሱት የሚኒስቴሩ ከፍተኛ ሓላፊዎች፣ ‹‹ የሕዝብ ሀብት ለህዝብ ጥቅም መዋል አለበት፤ በሕዝብ ገንዘብ እንዲቀለድ አንፈልግም፤ መንግሥት ሰላምንና የሕግን የበላይነት ከማረጋገጥ አኳያ ደረጃውን ጠብቆና የሙስና ወንጀል መፈጸሙን አጣርቶ ርምጃ ይወስዳል፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ሙዳየ ምጽዋቱን ማን ነው የሚጠቀምበት፤ ሕዝብ ይጥላል፤ ጥቂት ሰዎች መኪና እና ቤት ይሠሩበታል፤›› በማለት የአለመግባባት መንሥኤዎችን የዘረዘሩት ሚኒስትር ዴኤታው አቶ ሙሉጌታ ውለታው፣ የሚዘርፉት ሃይማኖት ሳይኖራቸው በሃይማኖት ስም የሚነግዱ ግለሰቦች እና አካላት እንደኾኑ ገልጸዋል፡፡ በሚፈጽሟቸው ወንጀል ነክ ጉዳዮችም ‹‹መንግሥት ለምን ጣልቃ ይገባል አይባልም፤ ከሀገረ ስብከቱ ጋር ኾኖ ይከታተላል፤ ወንጀለኛውን ይይዛል፤ ይቀጣል፤ ያጸዳል፤›› ብለዋል፡፡
የግልጽነት እና የተጠያቂነት አሠራር ዘመኑ የሚጠይቀው እና መንግሥትም በአቋም ያስቀመጠው መኾኑን ያወሱት ሚኒስትር ዴኤታው፣ የሀገረ ስብከቱ ሰንበት ት/ቤቶች ሙስናና ብልሹ አሠራር እንዲወገድ፣ መልካም አስተዳደር እንዲሰፍንና ሃይማኖት እንዲጠበቅ የጀመሩትን እንቅስቃሴ አድንቀዋል፡፡ ‹‹እንቅስቃሴአችኹን ከሁከት በራቀ፣ ስልታዊ በኾነና በሰላማዊ መንገድ ቀጥሉ፤ መንግሥትም ድጋፍ ያደርግላችኋል፤›› ሲሉም አበረታተዋቸዋል፡፡
የሰንበት ት/ቤት አባላት ሰላም ፈላጊዎች እንደኾኑ የገለጹት የአንድነቱ አመራሮች በበኩላቸው፣ ለቤተ ክርስቲያን ሰላም መደፍረስ ዋነኛ ምንጩ የመልካም አስተዳደር ዕጦት እንደኾነ አስረድተዋል፡፡ እንደ አመራሮቹ፣ ቅዱስ ሲኖዶሱ እና ቅዱስ ፓትርያርኩ ሙስናንና ብልሹ አሠራርን ለማስወገድና ተቋማዊ ለውጥን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ውሳኔዎችን በየጊዜው ቢያሳልፉም ትግበራው አስተዳደራዊ መዋቅሩን ከላይ እስከ ታች በኔትወርኪንግ በተቆጣጠሩ ሙሰኞች ስለሚታገት ተፈጻሚ ለመኾን አልቻለም፡፡
ሙሰኞቹ÷ በሙዳየ ምጽዋት፣ በስእለትና በስጦታ ምእመኑ የሚሰጠውን ገንዘብ ለራሳቸው ዓላማና ጥቅም እያዋሉ፤ የአድባራቱን መሬትና ሕንፃ ከዋጋ በታች እያከራዩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ጥቅሞችና መብቶች ከገቢያቸው በላይ ሕገ ወጥ ሀብት ያካብታሉ፤ በሦስትና በአራት ሺሕ ብር ደመወዝ ኤሮትራከር ይገዛሉ፤ ሕንፃ ይሠራሉ፡፡
ይኹንና የተጠያቂነትና የግልጽነት አሠራር ባለመኖሩ ሲነቃባቸውና ተቃውሞ ሲበረታባቸው የበለጠ ወደሚዘርፉበት ቦታ በዕድገት እንደሚዘዋወሩ ጠቅሰው፣ ለዚኽም በጎጠኝነትና በጥቅም ትስስር ተሞልቷል ያሉት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ፅ/ቤት ተጠያቂ ነው ብለዋል፡፡ “ሀገረ ስብከቱ ሌባን አሳልፎ አይሰጥም፤ በሹመት እና በዝውውር ጉቦ እየተከፈለ አብሮ ይበላል፤” በማለት የወቀሱት አመራሮቹ፣ “የሕዝብ ንብረት እየባከነ ስለኾነ መንግሥት ጣልቃ ይግባልን፤ የመንግሥት ባለሥልጣናት ሀብታቸው ተሰፍሮ ተቆጥሮ ይታወቃል፤ አሠራሩ እዚኽም ይምጣልን፤” ሲሉ አመልክተዋል፡፡
ሙሰኞችን በመቃወማቸውና እውነቱን በመናገራቸው አሸባሪዎች ተብለው ለእስር እንደሚዳረጉ  አመራሮቹ ጠቁመው፣  የጸጥታ አካላት ርምጃ ከመውሰዳቸው በፊት ኹኔታቸውን በሚገባ እንዲያጣሩና ፍትሐዊ አሠራር እንዲከተሉ ጠይቀዋል። ከአስተምህሮ ውጭ የኾኑ ግለሰቦችን የማጋለጥ ድርሻ የእነርሱ መኾኑን ገልጸው፣ በዚኽም በአክራሪነት መፈረጃቸው አግባብነት እንደሌለው ተናግረዋል፡፡
“አክራሪነትና ጽንፈኝነት በሃይማኖት ተቋማት ውስጥ መኖሩ የሚያከራክር አይደለም፤” ያሉት ሚኒስትሩ ዶ/ር ሺፈራው ተክለ ማርያም፣ ኾኖም ጥያቄው በሃይማኖት አጥባቂነት እስከተነሣ ድረስ ከአክራሪነት ስለሚያርቅና ከሙስና ስለሚጠብቅ የሚደገፍ መሆኑን ጠቁመው የፍረጃው አካሔድ ስሕተት መኾኑን አብራርተዋል። እንደ ሚኒስትሩ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተምህሮ የማይፈቅደውን የአክራሪነት አስተሳሰብና ተግባር በሃይማኖት ሽፋን የሚያራምዱ ግለሰቦች ለተቋሙ ደኅንነት ሲባል መለየት አለባቸው፡፡
ሕዝብ ከተግባርም እንደሚማር ዶ/ር ሺፈራው ገልጸው፣ አትስረቅ እያሉ በሌላቸው ገቢ የሚልዮን ብር መኪኖችን የሚነዱ አካላት፣ ለሀገር መልካም ዜጋ የምታወጣውን ተቋም በማማሰን በሕዝብ ላይ ተጽዕኖ እየፈጠሩ ናቸው ብለዋል፡፡ ይህም ለሀገር የሚጎዳ በመኾኑ ድንጋይ በመወርወር ሳይኾን በምእምኑ ሰላማዊ እንቅስቃሴ በቀጣይነት መጋለጥ እንደሚገባቸው መክረዋል፤ የሰንበት ት/ቤት አባላትም ከቤተ ክርስቲያኒቷ አልፎ ለሀገርና ለዓለም የሚበቁ ሊቃውንቷን በማስተባበር ለመልካም አስተዳደር መስፈን የሚያደርጉትን ጥረት አጠናክረው እንዲቀጥሉ አሳስበዋል፤ መንግሥትም ‹‹መዋቅሩን ጠብቆ በወንጀሉ ላይ ይገባል፤ በሕግም ይጠይቃቸዋል፤ በሃይማኖቱ መሸፈን አይችሉ፤›› ሲሉ አስታውቀዋል፡፡
በሚኒስቴሩ የስብሰባ አዳራሽ በተደረገው በዚኹ የግማሽ ቀን ምክክር ማጠናቀቂያ ላይ፣ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የዋና ክፍል ሓላፊዎች የተገኙ ሲኾን ሚኒስትሩም “የወጣቶቹን ጥያቄ እንደ ቀላል አትዩት፤ በአስቸኳይ ፍቱ” ሲሏቸው ተደምጠዋል፡፡
ቀደም ሲል ሚኒስቴሩ፣ ከሀገረ ስብከቱ የአድባራት አለቆች፣ ካህናት እና ሰባክያነ ወንጌል ጋር ተመሳሳይ ምክክር ያደረገ ሲሆን፤ ይኸውም በቅርቡ በሃይማኖት ተቋማት በሰላም አብሮ መኖር እና ጤናማ ግንኙነቶች ማስፈንን በተመለከተ በጋራ እንደሚካሔድ ለሚጠበቀው ውይይት ቅድመ ዝግጅት እንደኾነ ተጠቁሟል፡፡

Published in ዜና

የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር በአገር አቀፍ ደረጃ የንባብ ባህል እንዲዳብር “ከመንግሥት እና ከባለድርሻ አካላት ምን ይጠበቃል?” ለሚለው ጥያቄ መልስ ለመስጠት የሚያስችል አውደ ጥናት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአማርኛ ቋንቋ ሥነ - ፅሁፍና ፎክሎር ትምህርት ክፍል ጋር በመተባበር በትላንትናው ዕለት በብሄራዊ ቤተ መዛግብት እና ቤተ መፃህፍት ኤጀንሲ አዳራሽ አውደ ጥናት አካሂዷል፡፡ በአውደ ጥናቱ ላይ አቶ ደረጀ ገብሬ (ረ/ፕ) “የንባብ ባህልን ለማዳበር የባለድርሻ አካላት ሚና” በሚል ርዕስ እንዲሁም ዶ/ር ሙሉ ሰው አስራቴ፤ “የልሳነ ብዙ የቋንቋ ትምህርትና ፖሊሲ የንባብ ባህልን ለማዳበር የሚኖረው ተግዳሮት እና ዕድል” በሚል ርዕስ የውይይት መነሻ ሃሳቦችን ማቅረባቸው ታውቋል፡፡

Published in ዜና

  በአሌክስ አብርሐም በተፃፈው “ዶ/ር አሸብር” የተሰኘው የወግ ስብስቦች መፅሃፍ ላይ በነገው ዕለት ከ8 ሰዓት ጀምሮ በወ-መዘክር አዳራሽ ውይይት ይካሄዳል፡፡ ለውይይት መነሻ የሚሆን ሃሳብ የሚያቀርበው ደራሲና ጋዜጠኛ አለማየሁ ገላጋይ ነው ተብሏል፡፡
የመፅሃፍ ውይይቱ እናት ማስታወቂያ፣ የጀርመን የባህል ማዕከልና ወመዘክር በጋራ የሚያዘጋጁት እንደሆነ ታውቋል፡፡