Monday, 24 August 2015 09:52

“…ነግረኸዋል?”

    ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ እኔና ባለቤቴ የገጣሚ ተፈሪ ዓለሙን የግጥም መጽሀፍና የግጥም ሲዲ ለመመረቅ በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ ተገኝተናል፤ ከሌሎች በርካታ እንግዶች ጋር፡፡
ወደ ቀኜ ዞር ስል የማስታወቂያ ባለሙያውን ተስፋዬ ማሞን አየሁትና በአንገት ዝቅታ ሰላም አልኩት፡፡ እሱ ከወንበሩ ብድግ ብሎ በወንበሮቻችን መካከል ያለውን ሸለቆ ተሻግሮ በመምጣት ሁለታችንንም ጨብጦ ወደ ወንበሩ ተመለሰ፡፡ የተስፋዬ የሰላምታ ሙቀትና ትህትናው ደስ የሚያሰኝ ነበር፡፡
ወደ ባለቤቴ ዞሬ፤ “ተስፋዬ ደስ ይለኛል” አልኳት።
“ነግረኸዋል?” አለችኝ፤ በፍጥነት፡፡
“አልነገርኩትም” አልኳት፡፡
እኔና ባለቤቴ ይህን ተባብለን ስናበቃ ወደ ጀመርነው ጨዋታ መለስ አልን፡፡ ሆኖም፤ “ነግረኸዋል?” የሚለው ጥያቄ ዕረፍት ስለነሳኝ ከወንበሬ ተነሳሁና አንድ እርምጃ ተራምጄ ከጎኑ በመቆም፤ እሱ እንደተቀመጠ፤ “ተስፍሽ” አልኩት። “ባለቤቴ፤ በለጠችኝ፤” አስከትዬም ከእስዋ ጋር የተባባልነውን በሹክሹክታ ነገርኩትና ተሳስቀን፣ ስሜቴን ስለነገርኩትም አመስግኖኝ ወደ ወንበሬ ተመለስኩ፡፡
ከዚያ “ነግረኸዋል?” የሚለው ጥያቄ ራሱን በራሱ ማባዛት ጀመረ፡፡ “ነግረኻቸዋል?” ብሎ ይጠይቀኝ ጀመር ከውስጤ የሚሰማኝ ድምጽ፡፡ በሕይወት ዘመኔ እንደምወዳቸው፣ እንደማደንቃቸው ያልነገርኳቸው ሰዎች በአይኔ ላይ በሰልፍ ተመላለሱ፡፡ አንደኛው አቶ መንግሥቱ መኩሪያ ናቸው፡፡
ፍቀዱልኝና ስለኚህ ሰው ልንገራችሁ፡፡ አቶ መንግሥቱ የኛ ሰፈር ልጆች ሆያሆዬ ለመጫወት ወደ ቤታቸው በሄድን ቁጥር (ክብረመንግሥት)፣ አንድም አመት ሳያጎድሉብን፤ ከኪሳቸው መዘዝ አድርገው “አንድ ብር” የሚሰጡን ሰው ነበሩ፡፡ ይታያችሁ፤ በዚያን ጊዜ ትልቁ የቡሔ ስጦታ ቢበዛ ሀያ አምስት ሳንቲም ነበር፡፡
ሰውየው ብር ከመስጠታቸው በላይ ደስ ያሰኘን የነበረው ብሩን ከሰጡን በኋላ እንደ ሌሎቹ አባወራዎች ብዙ ጨፍሩልኝ የማይሉ ሰው መሆናቸው ነው፡፡ እርግጥ ነው፤ እሳቸው ብዙ እንድንጨፍር ባይጠብቁም፣ እኛ በአፋችን “ሆያ ሆዬ” ከማለት አልፈን፤ ሀርሞኒካ እየነፋን ቤታቸውን እናደምቅ ነበር። ቤታቸው ደግሞ ወለሉ ጣውላ በመሆኑ በዱላ ሲደቀደቅም ሆነ ሲጨፈርበት ጥሩ ያዳምቅ ነበር፡፡
አቶ መንግሥቱ የሆያሆዬ ጊዜ ተስፋችን ብቻ አልነበሩም፡፡ የሰፈር ልጆች ለከፍተኛ ትምህርት ወደ ሌላ ከተማ ለመሄድ ጎረቤቶቻችንን እየዞርን ስንሰናበትም ሁለት ብር (በተማሪ) መዥረጥ አድርገው ያሽጉ (ን) የነበሩ ሰው ናቸው፡፡ ችሮታና “ጎሽ”ታቸው ወደር አልነበረውም፡፡ “በዚያን ጊዜ ሁለት ብር ምን ይገዛ ነበር?” የምትሉ አንባቢያን ካላችሁ፣ ያ ገንዘብ አጭሬው ከጭብጥ የሚያልፍ አውራ ዶሮ (ቀይ፣ ወሠራ፣ ገብስማ … ነጠላ፣ ድምድም ራስ … በአይነት) ባለቤት ያደርጋችሁ ነበር እላችኋለሁ፡፡
አንዴ እሺ ብላችሁኛል፤ ከአቶ መንግሥቱ መኩሪያ ጋር ከተያያዙ የግል ትዝታዎቼ ትንሽ ልጨምርላችሁ።  ትልቅ ከሆንኩ፣ ስራ ከያዝኩ፤ ደሞዝተኛ ከሆንኩ፤ ወዲህ ሁሉ ወደ አገር ቤት ስሄድ አቶ መንግሥቱ ቢራ ይጋብዙኝ ነበር፡፡ በስሜት ከልጅነቴ ውስጥ ባለመውጣቴ ግን “እኔ ልክፈል” ማለት ያስፈራኝ ነበር።
ታዲያላችሁ፤ ከጥቂት አመታት በኋላ “ነፍስ አወቅሁ”ና አገር ቤት ስሄድ ለማድረግ ካቀድኳቸው ነገሮች መካከል አንደኛው፤ አቶ መንግሥቱ መኩሪያን በክብረመንግሥት ከተማ ውስጥ አለ ወደሚባል ሆቴል ወስዶ ራትና ቢራ መጋበዝ ሆነ - እና ደግሞ እኔም ሆንኩ የሠፈራችን ልጆች ሁሉ እንደምንወዳቸው፣ እንደምናከብራቸውና እንደምናደንቃቸው መንገር፡፡ እኚህ ሰው ድፍን አንድ ብር ከኪሳቸው አውጥተው፣ እጃቸውን ከአናታቸው በላይ ከፍ አድርገው ሲያሳዩን ይሰማን ስለነበረው ሀሴት፤ ምን ይሄ ብቻ? የእንጨት መሰንጠቂያ ፋብሪካ ሠራተኛ ቢሆኑም የልብሳቸው ፅዳትና ንፅህና ምን ያህል ይማርከን እንደነበር፤ እያሳሳቅኹ መንገርም ሆነ እቅዴ፡፡
ታዲያላችሁ፤ አንደበቴን ለምስጋናና ለሙገሳ አዘጋጅቼ፣ ኪሴን በብር አጭቄ ወደ አገር ቤት ስሄድ አቶ መንግሥቱ መኩሪያ በህይወት አልነበሩም፡፡ እኒያ ደግ ሰው በታመሙ ጊዜ እንዴት ሳልሰማ፣ ማለቴ እንዴት ሳይነገረኝ ቀረ? ብዬ አዘንኩ፡፡ ያው ባዳ ስለሆኑ ነው አይደል? የባዳ መርዶ በየሜዳው ነውና በሰማሁ ጊዜ እሪ ብዬ አለቀስኩ፤ ልቤ ተሰበረ፡፡ እነሆ፣ እስከዛሬ ድረስ ሳስታውሳቸው ስሜቴ ይደፈርሳል፡፡ ምክንያቴ ግልጽ ነው፤ “አልነገርኳቸውም፡፡”
ወደዚያው ወደ ብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ ልመልሳችሁና ባለቤቴ የሰራች(ው)ኝን ሌላ ነገር ልንገራችሁ፡፡ ነገሩ ከተነሳሁበት ርዕስ ጋር በጥሩ ሁኔታ አብሮ የሚሄድ ነው፡፡
ዝግጅቱ አለቀና በክብር ወደ ተጋበዝንበት የቴአትር ቤቱ የኮክቴል አዳራሽ በመሄድ ላይ እያለን ባለቤቴ አርቲስት ሐረገወይን አሰፋን ከማየትዋ ተወርውራ አንገትዋ ላይ ተጠመጠመችባት፡፡ ሁለቱ እቅፍቅፍ ብለው ይሳሳሙ ጀመር፡፡ ከዚህ ቀደም የሚተዋወቁ ስለመሰለኝ የበኩሌን እንደማደንቃት (በተለይ፣ በተለይ በአንድ የሬዲዮ ትረካዋ ምን ያህል እንዳደነኩዋት) ነግሬያት ተለያየን፡፡
አለፍ እንዳልን “ትተዋወቃላችሁ ለካ!” አልኩዋት ባለቤቴን፡፡
“እንዲያውም፤ አንተዋወቅም!” አለችኝ፡፡
“እና …” አልኩዋት፤ መተቃቀፉ ከየት የመጣ ነው? ልላት ብዬ፡፡
“ላሳይህ ብዬ ነዋ!” አለችኝ፤ እየሳቀች፡፡
“ምኑን?” አልኩዋት፡፡
“የሚያደንቁትን ሰው እንዴት እንደሚነግሩት ነዋ” አለችኝ፡፡ እንዲህ እቅፍ አድርጎ ስሞ መንገርም አለ ማለትዋ ነው፡፡
የሚገርመው፣ ከዚህ ቀደም ከባለቤቴ ጋር በአንድ ዝግጅት ላይ ታድመን ሳለ አንዲት ታዋቂ አርቲስት ከአጠገብዋ ተቀምጣ ምንም ስላላለቻት “ምነዋ ዝም አልሻት?” ስላት “አላደንቃትም፡፡ የማላደንቀውን ሰው ደግሞ ‹አድናቂሽ ነኝ ብዬ› አልሸነግልም፤ ራሴንማ አላታልልም” ነበር ያለችኝ፡፡
ወደዚሁ ዝግጅት ለመጨረሻ ጊዜ መለስ ልበልና ሌላ ማድነቄን ስለነገርኩት ሰው ላጫውታችሁ። የእለቱ ዝግጅት ወሳኝ ሰው ጋዜጠኛ ደረጃ ሀይሌ ነበር፡፡ ምርጥ የመድረክ አስተዋዋቂ፣ ድሮና ዘንድሮን አያያዥ፣ አድንቆ አስደናቂ፣ የተረሱ እንቁዎቻችንን፤ ለምሳሌ (ታደሰ ሙሉነህን - በስም ካልጠራሁ እንዳይቀየመኝ ብዬ ነው) አስታውሶ አሞጋሽ ሆኖ ነው ያመሸው፡፡ የእለቱን “ሙሽራ” ተፈሪ ዓለሙን፣ እንዲሁም ሌሎች ሰዎችን በስም ሲጠራ የቤት ስራውን በሚገባ ሰርቶ እንደመጣ ምስክር አያሻውም። በድምጹ ብቻ ሳይሆን በሞቀ ስሜትም አዳራሹን ከዳር እስከ ዳር፣ ከጥግ እስከ ጥግ፣ ከወለል እስከ ጣሪያ የሞላ ሰው ነበር፤ ደረጀ፡፡
ደረጀ አያውቀኝም፡፡ የማውቀውና የማደንቀው እኔ ነኝ፡፡ ስልኩን ከየት ላገኝ እንደምችል ሳስብ ቆይቼ ለታገል ሠይፉ በሞባይሌ የጽሁፍ መልዕክት ልኬ፣ የስልክ ቁጥሩን እንዲልክልኝ ጠየኩት፡፡ ላከልኝ፡፡ አመሰግነዋለሁ፤ ታገል (ልንገርህ ብዬ ነው)!
በማግስቱ ለደረጀ ደወልኩለት፡፡ አላነሳም። ጥቂት የአድናቆት ቃላትን ጽፌና ማንነቴን ገልጬ ተልዕኮዬን አበቃሁ፡፡ ትንሽ ቆይቶ ደረጃ ደወለ፡፡ በድምጹ ለየሁት፡፡ የ”ነግረኸዋል?”ን ታሪክ ነገርኩት፡፡ ተሳሳቅን፡፡ እሱም ብዙ “ያልነገራቸው” ሰዎች በሞት እንዳመለጡት አጫወተኝ፤ እንደሚቆጨውም ጭምር፡፡ ጎበዝ፤ እናንተስ? “ነግረኸዋል? የሚለው ጥያቄ ማንን አስታወሳችሁ? አለመንገር ትልቅ የህሊና ሸክም ነው (አለኝ መሰለኝ ደረጀ)፡፡

Published in ህብረተሰብ

‹‹የመድሃኒት ጥቂት ይበቃል እያለች
የምኒሊክ እናት አንድ ወልዳ መከነች››
(ሰርጉ ሃብለስላሴ)
‹‹የሸዋው ንጉስ ሣህለ ሥላሴ ‹ምኒሊክ› በሚባል ስም ሊነግሱ ሲሉ አንድ መነኩሴ ‹በዚህ ስም አትንገስ፣ መጥፎ አጋጣሚ ያመጣብሃል፡፡ ይህ ስም የሚስማማው ከመጀመሪያ ልጅህ ከኃይለ መለኮት ለሚወለደው ነው። ይህም ስም የሚወጣለት የልጅ ልጅህ ኢትዮጵያን አንድ የሚያደርግ ትልቅ ንጉስ ይሆናል…›› ይል ነበርና ክብረ ነገስቱ፣ ንጉስ ሳህለ ሥላሴ ‹ምኒሊክ› በመባል የመንገሳቸውን አሳብ ተዉት፡፡ ይህ ከሆነ ከብዙ ዓመታት በኋላ፣ የአንኮበር ቤተ ክርስቲያን አለቃ የነበሩት የመምህር ምላት ገረድ፣ እጅጋየሁ ለማ አዲያሞ፣ የተባለች ሴት አንድ ቀን ጠዋት ‹‹ዛሬ በህልሜ ከብልቴ ፀሃይ ስትወጣ አየሁ…›› ብላ ብትናገር፣ ወሬው ከአለቃ ምላት ይደርስና ‹‹ወደ ላይ ቤት ትሂድ›› ተብላ ለንጉሥ ሳህለ ሥላሴ ሚስት ወ/ሮ በዛብሽ ተሰጥታ የቤተመንግስቱ ገረድና የልጆች ሞግዚት ትደረጋለች፡፡
ይህን ወሬ የሰሙት ወ/ሮ በዛብሽ፣ ያ በህልም የታየው ፀሃይ ከልጃቸው እንዲወለድ ስለፈለጉ አብዝተው ለሚወዱት ለሰይፉ ሳህለ ሥላሴ እጅጋየሁን ‹አጥበውና አጥነው› ወደ ሰይፉ መኝታው ይሰዷታል፡፡ ወሬውን ቀድሞ የሰማው ሰይፉ፣ የሚወዳት ሌላ ሴት ነበረችውና፣ ወንድሙን ሃይለ መለኮትን ‹‹እባክህን ሌላ ሴት ከሌለህ እሜቴ የላኳትን ያቺን ገረድ ውሰድልኝ›› ብሎት ተስማሙና፣ እጅጋየሁ በዚያች ምሽት ከሃይለ መለኮት ትፀንሳለች፡፡
የእርግዝናዋ ወሬ ይፋ ሲሆን ወ/ሮ በዛብሽ ከሰይፉ ሳይሆን ከሃይለ መለኮት በማርገዟ፣ ንጉስ ሳህለ ሥላሴ ደግሞ ልዑሉ ልጃቸው ገረድ በማስፀነሱ ሁለቱም ተናደዱ፡፡ እጅጋየሁም ከነቅሪቷ የንጉስ ሳህለ ሥላሴ እርስት ወደ ነበረው ወደ አንጎለላ ሄዳ በግዞት እንድትቀመጥ ተፈረደባት፡፡
ቅዳሜ ነሐሴ 12፣ 1836 ዓ.ም እጅጋየሁ በአንጎለላ ቤቷ ወንድ ልጅ ተገላገለች፡፡ እዚያው እቤቷ ጓሮም የልጇ እትብት ተቀበረ፡፡ ይህን የሰሙት ንጉስ ሳህለ ሥላሴም፣ ‹ልጄ አዋርደኸኛል፣ እንግዲህ ሸዋ ምን ትለኝ ይሆን…?› በሚል መሳይ ቁጭት የልጁን ስም ‹‹ምን-ይልህ-ሸዋ›› ብለው ጠሩት፡፡
ኋላም አንድ ቀን በህልማቸው ከዚህ ብላቴና ጋር አብረው ቆመው ሳለ፣የልጁ ጥላ ከሳቸው ጥላ ገዝፎ ይታያቸዋል፡፡ መሬት የረገጠው የእግሩ ምልክት፣እሳቸው ከረገጡት በላይ ረዝሞ ቢያዩት ጊዜና ከእንቅልፋቸው ሲነቁ፤‹‹ምኒሊክ የኔ ስም ሳይሆን የሱ ነው፡፡ ይህንን ልጅ ስሙን ‹ምኒሊክ› በሉት ብለው አዘዙ፡፡›› ይለናል ጳውሎስ ኞኞ፣ አጤ ምኒልክ በሚለው መፅሃፉ ላይ፡፡
ይህ ከሆነ ከ171 ዓመታት በኋላ ነሐሴ 12 ቀን 2007 ዓ.ም የታሪክ ፀሃፊና ተመራማሪ በሆነው ወጣት ዳንኤል በላቸው ፊታውራሪነትና በገጣሚ ኤፍሬም ስዩም፣ ገጣሚ ደምሰው መርሻና በጋዜጠኛ/ገጣሚ ባንቺአየሁ አለሙ ደጀንነት፣ ምኒሊክ ወደዚህ ዓለም የመጡባትንና እትብታቸው የተቀበረባትን ኩርባ መሬት፣ በልደት ቀናቸው ለመዘከር፣ ራሳቸውን ጨምሮ 15 ሰዎችን በማሰባሰብ፣ ከጠዋቱ 1፡30 ላይ ጣይቱ ሆቴል በር ላይ ለጉዞ ተዘጋጅተው ነበር፡፡  
ምንተስኖት ማሞ (ገጣሚ)፣ አሌክሳንደር በየነ (ገጣሚና የዋሊያ ቢራ ባልደረባ)፣ ብሩክ ሞገስ (ኢንጂኒየር)፣ መስፍን አይንካው(የአማኑኤል የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ተቋም ባለቤትና የመጪው ዓመት ጉዞ ስፖንሰር)፣ ዘላለም አበራ (የካሜራ ባለሙያ)፣ ብርሃኑ አየለ (ገጣሚና የማስታወቂያ ባለሙያ)፣ ሰናይት አዱኛ (የዓለም ዓቀፍ ግንኙነት ባለሙያ)፣ ጌቱ ኦማሂሬ (ድምፃዊ)፣ ተወልደ ብርሃን ኪዳኔ (ሰዓሊ)፣ ጌታቸው እሸቱ (መምህር) እንዲሁም እኔ ጥላሁን አበበ የተጓዥ ቡድኑ አባላት ነበርን፡፡
ጉዞአችን በምኒሊክና በሌሎች ጠለቅ ባሉ ታሪካዊ ውይይቶች እንደታጀበ ነበር ረፋዱ ላይ ሸኖ ከተማ የደረስነው፡፡ ለቡና እረፍት እያደረግን ሳለ ግን አንድ ያልጠበቅነው መጥፎ ክስተት ተፈጠረ፡፡ የተሳፈርንበት ኮስትር-ሚኒባስ የቴክኒክ ብልሽት ገጠመውና ጉዞአችን የተስተጓጎለ መስሎን ብዙዎቻችን ተጨነቅን፡፡ የጭንቀታችን ዋናው ምክንያት፣ የዚያን ቀን ማታ በ11፡00 ሰዓት ላይ በፑሽኪን አዳራሽ የገጣሚ አደም ሁሴን መፅሐፍ ስለሚመረቅና እኔን ጨምሮ ቢያንስ 4 ገጣሚያን የመድረኩ አጋፋሪዎች ስለነበርን ነው፡፡ ጌታቸው እሸቱ ደግሞ የፕሮግራሙ አስተባባሪ ስለነበር ብቸኛው አማራጭ በሚኒባስ ወደ አዲስ አበባ መመለስ ብቻ ሆነ፡፡ ወዲያው ግን ከፍተኛ ቅናሽ አድርጎ የተባበረን የመኪናው ባለቤት፣ ሙሉ ክፍያችንን መልሶልን በሌላ ሚኒባስ ኮንትራት እንድንሄድ ስላስቻለን፣እሱን እያመሰገንን ጉዞአችንን በደብረ-ብርሃን አድርገን ወደ አንጎለላ ቀጠልን፡፡
ከቀኑ 6፡00 ገደማ ላይ ጭር ካለ አካባቢና ዙሪያ ገባውን የተሰበጣጠሩ ነዋሪዎች ካሉባት አንጎለላ መንደር ስንደርስ አይናችንን የሳበው፣ አንድ እንደነገሩ በሽቦ የታጠረ የጤና ጣቢያ ግቢ ውስጥ ያለ የድንጋይ ማማ ነው። በማማው አናት ላይ ደግሞ ከወገብ በላይ የተቀረፀና ሻሽ የጠመጠመ የምኒሊክ ሃውልት ከነምኒሊካዊው ግርማ ሞገሱ ጉብ ብሏል፡፡ የቡድኑ መሪ በሰጠን ማብራሪያ መሰረት፣ ያቺ ሀውልቱ የተሰራባትና የቆምንባት መሬት፣ የወ/ሮ እጅጋየሁ የግዞት ጎጆ የተቀለሰባት፣ብሎም ምኒሊክ በንግስና ዘመኑ ‹‹ማርያምን…!›› ብሎ አገርን አንድ ከማድረጉ በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ ድምፁን በልቅሶ ያሰማባት እንደሆነች ስንረዳ በሁላችንም ውስጥ አንዳች ኩራት ሞልቶን ነበር፡፡  
የጉዞአችንን መርሃ ግብር ለማከናወን፣ ለምኒሊክ ውልደተ ክብርና ዝክር የገዛነውን አበባ በማስቀመጥና ሻማ በማብራት ጀምረን ስናበቃ፣የተወሰንነው ስነፅሁፋዊ ሥራዎችና ታሪካዊ ስነ-ቃላት አጠር አጠር አድርገን አቀረብን፡፡
የታሪክ ባለሙያው ዳንኤል በላቸው፤ለምን ይህንን ልዩ ጉዞ እንዳዘጋጀ ካቀረበልን ዋነኛ ምክንያቶች መካከል ሶስቱን ስንመለከት፡- 1)በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የተወለደበት (ብሎም እትብቱ የተቀበረበት) እና በሞት ያረፈበት ቦታ በትክክል የሚታወቅ ንጉስ አፄ ምኒሊክ በመሆኑ፡፡ 2)ላለፉት 171 ዓመታት፣ ምናልባት የመካነ መቃብሩ ቦታ እንጂ ይህ የውልደት ቦታው አንዴም በገሃድ ያልተጎበኘ በመሆኑ፡፡ እንዲሁም 3) በአጠቃላይ ምኒሊክ እንደ ትንቢቱ ኢትዮጵያን አንድ በማድረግ ብቻ ሳይገታ፣ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ባለው የላቀና ታሪካዊ አስተዋፅዖው ምክንያት እንደሆነ አስረድቶን ሲያበቃ፣ወደፊትም በየዓመቱ ጉብኝቱ ከአሁኑ በበለጠ ሁኔታ በስፋት እንደሚቀጥል ተናግሯል፡፡  
ባንቺአየሁና ሰናይት፣ አፄ ምኒሊክ ከተፃፃፏቸው ደብዳቤዎች መካከል ለእቴጌ ጣይቱ የፃፉትን ፍፁም ፍቅር አዘል ደብዳቤዎች ሲያነቡልን፣ምኒሊክ ለሚስታቸው የነበራቸው ፍቅርና አክብሮት ምን ያህል ጥልቅ እንደነበር በግልፅ ለመረዳት ችለናል፡፡ ብርሃኑና አሌክሳንደር፤ በምኒሊክ ላይ ከተፃፉት የታሪክ መጻህፍት መካከል ከአንደኛው ላይ ጥቂት አንቀፆችን ያነበቡልን ሲሆን ገጣሚ ኤፍሬም ስዩም፣ በጣም ከምናውቀውና ከተወደደለት ‹‹የምኒሊክ አናት›› የተሰኘ ግጥሙ ላይ የተወሰኑ ስንኞችን በቃሉ ሲወርድልን፣ሁላችንም በውስጣችን የምኒሊክ መንፈስ አድሮብን ነበር፡፡
እኔም ‹ምኒሊክ አሁን ከሞት ተነስቶ ቢያይ…› በሚል ጭብጥ በቅርቡ እየፃፍኩት ከነበረውና  ከምኒሊክ የሙት መንፈስ ጋር ካደረግኩት ውይይት ላይ ጥቂት አንቀፆችን ያነበብኩ ሲሆን  ምኒሊክ በሞት የተቀጡ ወንጀለኞችን ለመግደያ እንዲሆን ከአሜሪካ ካስመጧቸው 3 ወንበሮች መካከል አንዱን ለራሳቸው መቀመጫ ዙፋንነት ያገለግል ዘንድ የመውሰዳቸውን ነገር ስገልጽ፣ የጉዞው አባላት በሳቅ ዘና ብለው ነበር፡፡   
በመቀጠልም፣ከሃውልቱ በግምት 50 ሜትር ገደማ ወረድ ብለን የምኒሊክ እትብት የተቀበረባትን ቦታ ተመለከትን፡፡ ቦታዋ ለምልክት ያህል የድንጋይ ካብ ተከምሮባታል፡፡ እዚህ ሥፍራ ከ171 ዓመታት በፊት የአገር ንጉስ እትብት፣ መሬት ጫር ጫር ተደርጎ መቀበሩን  ስናስብ፣ሁላችንም ለዚህ ዕድል በመብቃታችን ከፍተኛ ደስታን ፈጥሮብን ካቧ ላይ ቆመን ፎቶ ተነሳን፡፡
በመጨረሻም፤ተሞጋግሰንና ተመራርቀን እንዲሁም ከዚህ በኋላ ሁላችንም ራሳችንን እንደ መስራች ኮሚቴ ቆጥረን፣ በየዓመቱ ይህንን መልካም አርዓያነት ሳናስተጓጉል ከዚህ በላቀ ሰፊ ስነ-ስርዓት እንደምናከብር ቃል በመግባት፣የመልስ ጉዞአችንን ጀመርን፡፡ ደብረብርሃን ላይ ምሳችንን በልተን በቀየርናት ሚኒባስ ሸኖ ከመግባታችን ጥቂት ደቂቃዎች ቀደም ብሎ የኮስትር- ባሱ ሹፌር መኪናውን በወጉ እንዳሰራው ስለጠቆመን፣ ባለ-ሚኒባሱን ሸኝተን በመጀመሪያው መኪናችን ጉዞ ወደ አዲስ አበባ ሆነ፡፡
 ማለዳ የተነሳንበት ጣይቱ ሆቴል በር ላይ የደረስነው 11፡30 ሲሆን በፑሽኪን አዳራሽ በሚካሄደው የወዳጃችን የመጽሐፍ ምርቃት ሥነስርዓት ላይ ለመታደም በቂ ጊዜ ነበረን፡፡
ዘንድሮ በ15 ተጓዦች የተጀመረው ተዘክሮ ልደት ምኒሊክ ወ ጣይቱ፤ወደፊት በብዙ ሰዎችና ግብሮች ታጅቦ እንደሚከናወንና ታሪካዊ ቦታውም የበለጠ ትኩረት ተሰጥቶት፣ የቱሪስት መስህብነቱ ከፍ እንደሚል መላ የጉዞ አባላቱ ተስፋ ያደርጋሉ፡፡

Published in ህብረተሰብ
Monday, 24 August 2015 09:49

የኪነት ጥግ

(ስለ ሙዚቃ)

- ማዜም የሚሹ ሁልጊዜ ዜማ አያጡም፡፡
የስዊዲሽ አባባል
- ለማዜም ምክንያት አያስፈልግህም፡፡
ማርቲ ሩቢን
- ነፍስህ ውስጥ ሙዚቃ ሲኖር፣ ሙዚቃህ ውስጥ
ነፍስ ይኖራል፡፡
ክሪስ ጃሚ
- ሙዚቃ ለነፍስ ጥንካሬ ያጎናፅፋል፡፡
ላይላህ ጊፍቲ አኪታ
- ማዜም እየቻልክ ለምን ታስባለህ?
ማርቲ ሩቢን
- እኔ ስፅፍ ነፍሴ ያዜማል፡፡
ሜሊሳ ማርሽ
- በትምህርት ቤት ከህፃናት ጋር ማዜሜ እጅግ
አስደሳች የህይወት ተመክሮዬ ነው፡፡
ፒቲ ሲገር
- ታላቅ ወንድሜ አሁንም ድረስ ከእኔ የተሻለ
ዘፋኝ እንደሆነ ያስባል፡፡
ሮድ ስቲዋርት
- ራሴን እንደ ሃገረሰብ ዘፋኝ አስቤ አላውቅም፡፡
ቦብ ዳይላን
- ሙዚቃ ሃይማኖቴ ነው፡፡
ጂሚ ሄንድሪክስ
- የዓለም እጅግ ዝነኛና ታዋቂ ቋንቋ ሙዚቃ ነው፡

PSY
- ሁሉም ሙዚቃ ውብ ነው፡፡
ቢሊ ስትራይሆርን
- በአሁኑ ጊዜ ፀጥታን የትም አታገኙም፡፡ ይሄን
ነገር አስተውላችኋል?
ብርያን ፌሪ
- የሆነ ጊዜ ላይ ልብህ ውስጥ ዜማ አይኖርም፡፡
እንዲያም ሆኖ ግን አቀንቅን፡፡
ኢሞሪ አውስቲን
- ልብህ ውስጥ ዛፍ አኑር፤ ምናልባት ዘማሪ ወፍ
ትመጣ ይሆናል፡፡
የቻይናውያን አባባል

Published in ጥበብ

ባለፉት አስር አመታት የተለያዩ ራስን የማበልጸግና የአመራር ስልጠናዎችን ለመካከለኛና ከፍተኛ አመራሮች በመስጠት የሚታወቀው SAK የስልጠና ማዕከል፤በዘንድሮ ክረምት 80 ለሚሆኑ ህጻናትና ወጣቶች እራስን የማበልጸግ (Personal Development)  ሥልጠና መስጠቱን አስታወቀ፡፡  
ስልጠናው በዋናነት ህጻናትና ወጣቶች ከትምህርት እውቀታቸው በተጨማሪ በባህሪያቸው ታንጸው በራሳቸው የሚተማመኑ፣አላማ መር ህይወት የሚመሩና ሃላፊነትን የሚቀበሉ የነገ አገር ተረካቢዎች እንዲሆኑ ለማስቻል ያለመ ነው ተብሏል፡፡
በሶስት ዙር በተሰጡት ስልጠናዎች ተሳታፊ የነበሩ ተማሪዎች እንዲሁም ወላጆች እርካታቸውን የገለጹ ሲሆን ስልጠናው በ10ኛው ቀን ሲጠናቀቅ የ“አልችልም አስተሳሰብ” የቀብር ስነስርዓት (“I can not do it; funeral) ይካሄዳል፡፡ የቀብር ስነስርአቱ ከመካሄዱ በፊት የሬሳ ሳጥን ይዘጋጅና ሁሉም ተማሪዎች ወደ ኋላ የሚያስቀሯቸው አስተሳሰቦች፣ ለምሳሌ - አልችልም፣ ይሉኝታ፣ ያበሻ ቀጠሮ፣ አይመለከተኝም፣ በጎ ነገሮችን ያለማድነቅ አባዜ፣ እኔ ብቻ ልጠቀም (win-Loss) ወይም ሁለታችንም አንጠቀም (Loss-Loss) ወዘተ---ተጽፈው በሳጥኑ ውስጥ ይገቡና ይቆለፍባቸዋል፡፡ በቀብሩ ስነስርዓት ወቅትም ተማሪዎች የደስታ ቀናቸው ስለሆነ፣ ሁሉም ነጭ ልብስ ለብሰው ወደ መቃብሩ ይሄዳሉ። በጉዞውም ላይ ቻው ቻው አልችልም፣ ባይ ባይ አልችልም የሚል መዝሙር ይዘምራሉ፡፡
የቀብሩን ጉድጓድ ተማሪዎች የሚያዘጋጁ ሲሆን የቀብሩም ቦታ ላይ የአልችልም አስተሳሰብ የቀብር ሥነስርዓት በንባብ ይሰማል፡፡ ከዚያም ሳጥኑ በጉድጓድ ውስጥ ገብቶ ይቀበራል፡፡ በቀብሩ ስነስርኣት ላይም ተማሪዎች እነዚህን የቀበሯቸውን ኋላ ቀር አስተሳሰቦች በድጋሚ እንዳያስቧቸው ቃል ይገባሉ፡፡ በቀብሩ ላይ የተነበበው ንባብ፣ በሰልጣኞች መኝታ ቤት ውስጥ እንዲለጠፍና ሁልጊዜ ተማሪዎቹ እንዲያዩት ይደረጋል፡፡
ሳይረፍድ በልጆቻችን አስተሳሰብ ላይ ለውጥ በማምጣት የወደፊት የህይወት መሰረታቸውን አብረን እንጣል የሚል ጥሪ ማስተላለፉን ያስታወሰው ማዕከሉ፤ጉዞውን በዘንድሮ ክረምት በስልጠና  መጀመሩን አመልክቷል፡፡ ስልጠናው መደበኛ ትምህርት በሚጀመርበት አዲሱ አመትም የሚቀጥል ሲሆን ቅዳሜና እሁድ እንዲሁም በየቀኑ የየእለቱ ትምህርት ከተጠናቀቀ በኋላ እንደሚሰጥ ማዕከሉ ጠቁሟል፡፡
የ SAK የስልጠና ማዕከል ራስን የማበልጸግ ስልጠናው እንደ ማንኛውም ትምህርት በአገራችን የትምህርት ስርአት ውስጥ ተካቶ ለሁሉም ኢትዮጵያዊ ተማሪ ከልጅነት ጀምሮ እንዲሰጥ ያለመ  ሲሆን ይህም ውጤቱ በእውቀትና በባህሪ የተገነባ ትውልድ ማፍራት ነው ይላል፡፡
የአልችልም አስተሳሰብ የቀብር ሥነስርዓት
እኛ ዛሬ እዚህ የተሰበሰብነው እራስን የማበልጸግ ሥልጠና የወሰድን ተማሪዎች፣ በዋናነት አልችልም የሚለውን አስተሳሰብና ሌሎችም እራስን ወደ ኃላ የሚያስቀሩ አስተሳሰቦችን ለምሳሌ፡-
እድለኛ አይደለሁም ብሎ ማሰብን
ለይሉኝታ መገዛትን
የአበሻ ቀጠሮ የሚባለውን ሰዓት የማርፈድ አስተሳሰብ
ሌላ ሰውን ለመምሰል የመፈለግ አባዜ
አይመለከተኝም የሚለውን አስተሳሰብ
አሉታዊ ጎኞች(Negative thinking) ላይ የማተኮር አስተሳሰብ
ድርድር ላይ መሸነፍ፣ መሸነፍ (Lose - Lose) የሚለውን ወይም የዜሮ ድምር አስተሳሰብ
ዛሬ ነሐሴ ----------/2007 ዓ.ም ከቀኑ 5 ሰዓት ላይ ቀብሬያቸዋለሁና ከዚህ በኋላ አነዚህ አስተሳሰቦች ከእኔ ጋር ቦታ የላቸውም፡፡ እነዚህ አሮጌ አስተሳሰቦች የአገራችን እድገት ጠንቅ በመሆናቸው በህይወት ዘመናችን ሁሉ ታግለን ከአገራችን ልናጠፋቸው ቆርጠን ተነስተናል፡፡ ዛሬ በቀበርናቸው አሮጌ አስተሳሰቦች ፋንታ የሚከተሉትን 10 አዲስ አስተሳሰቦች ለመተግበር ወሰነናል፡፡
እራሴን በቀጣይነት በእውቀት ለማሳደግ
እራሴን ተቀብዬ በማንነቴ ለመኩራት
በራሴ ለመተማመን
እችላለሁ በማለት በህይወቴ ለስንፍና ቦታ ላለመስጠት
በጎ አመለካከትን (Positive thinking) የህይወቴ መርህ ለማድረግ
የማድነቅ ባህልን የህይወት መመርያዬ ለማድረግ
ሃላፊነት መቀበልን ከህይወቴ ጋር ለማላመድ
የጋራ ተጠቃሚነትን ሁልጊዜ በህይወቴ ለመተግበር
ጊዜዬን በአግባቡ በመጠቀም ያበሻ ቀጠሮ የሚለውን አስተሳሰብ ለመሻር
ኑሮዩን በራይና በአላማ ለመምራት
ይህንንም የአልችልም አስተሳብ የቀብር ስነስርዓት ጽሁፍ፣ በመኝታ ቤቴ ግድግዳ ላይ ለጥፌ ሁልጊዜ ለማንበብ፤
ቃል እገባለሁ!
ቃል እገባለሁ!
ቃል እገባለሁ!

Published in ህብረተሰብ
Monday, 24 August 2015 09:47

የፀሐፍት ጥግ

ስለታሪክ)
- ሰው የህይወት ታሪኩን ለሌላ ሰው የተናገረ ዕለት
ነው ታሪክ የተወለደው፡፡
አልፍሬድ ዲ ቪጅኒ
- ጀግና ፈፅሞ የታሪኩ ኮከብ አይደለም፡፡
ማሪሊም ማንሶን
- ዩኒቨርስ የተሰራው ከአቶሞች ሳይሆን ከታሪኮች
ነው፡፡
ሙርየል ፋክይሰር
- ያልተነገረ ታሪክን በውስጥህ እንደመሸከም ያለ
ስቃይ የለም፡፡
ማያ አንጄሉ
- ሁሉም የየራሱ የህይወት ታሪክ ጀግና ነው፡፡
ጆን ባርዝ
- የሰው ልጅ በቆዳ የተለበጠ ታሪክ ነው፡፡
ፍሬድ አሌን
- ልብ ወለድ ፎቶግራፍ አይደለም፤ የዘይት ቅብ
ሥዕል ነው፡፡
ሮበርትሰን ዲቪስ
- ሁሉም ግሩም ታሪኮች አስር በመቶ እውነት
ናቸው፡፡
ኮሎኔል ዴኒስ ፋኒንግ
- ህብረተሰብን የሚገዙት ታሪክ ተራኪዎች
ናቸው፡፡
ፕሌቶ
- እያንዳንዱ የምፈጥረው ታሪክ እኔን ይፈጥረኛል፡፡
የምፅፈው ራሴን ለመፍጠር ነው፡፡
ኦክታቭ ያ ኢ. በትለር
- እውነቱን ለማወቅ የሁለቱንም ወገኖች ታሪክ
ማግኘት አለብህ፡፡
ዋልተር ክሮንኪት
- እያንዳንዷ ሴት የራሷ ታሪክ ባለቤት መሆን
አለባት፡፡ ያለበለዚያ ሁላችንም የዝምታው አካል
ነን፡፡
ዛይናብ ሳልቢ
- አገራትና ቦታዎች ታሪክ፣ ተረክና ባህል አላቸው።
ሞሼ ሳፍዲ
- ይሄን ታሪክ በፊት ሰምታችሁት ከሆነ
አታስቁሙኝ፡፡ ምክንያቱም ደግሜ ልሰማው
እሻለሁ፡፡
ግሮውቾ ማርክስ

Published in የግጥም ጥግ

ችግርንም ጫማንም እንጠርጋለን” ፕሮጀክት ይጀመራል

ባለፈው ረቡዕ ከሰዓት በኋላ የኢትዮጵያ ኮሜዲያን ማህበር አባላት ግማሽ ያህሉ ኮተቤ በሚገኘው “ሙዳይ በጎ አድራጎ ማህበር” ግቢ ውስጥ ነበሩ፡፡ ኮሜዲያኑ የተሰናዱበት ምንም ዝግጅት አልነበራቸውም፡፡ ከነሐሴ 11-17 ቀን 2007 ዓ.ም የቡሄንና የአሸንዳን በዓል ምክንያት በማድረግ በበጎ አድራጎቱ ማህበር ግቢ የተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚካሄድ በመስማታቸው ነበር ወደ ቦታው የመጡት።
በባህል ሳምንቱ የአሸንዳና ሆያ ሆዬ ጭፈራዎች እንደሚካሄዱ፤ የባህል ጥበቃ ላይ ያተኮረ ሲምፖዚየም መሰናዳቱን፤ የባህላዊ አለባበስ ትርዒት እንደሚቀርብ፤ የስዕል ኤግዚቢሽን እንደተሰናዳ፤ የችቦ፣ የዶሮና የእንቁላል ሽያጭ እንደሚኖር፤ በዝግጅቶቹ ላይም የተለያዩ አርቲስቶችና ታዋቂ ሰዎች እንደሚገኙ ሰምተዋል፡፡
በዚህ ምክንያት በ “ሙዳይ በጎ አድራጎ ማህበር” ግቢ የተገኙት ኮሜዲያኑ፤ በዕለቱ በግቢው የተሰናዳውን ዝግጅት አይተውና ገለፃ ሰምተው ብቻ መመለስ ስላልፈለጉ “ምን እናድርግ?” የሚል ጥያቄ አንስተው፣ በኮተቤ ዙሪያ የቡሄ ጭፈራ በመጫወት የበጎ አድራጎት ማህበሩን ሥራ ለማስተዋወቅ ወሰኑ፡፡
ለዚሁ ዓላማ በረከት በቀለ (ፍልፍሉ)፣ ደምስ ፍቃዱ (ዋኖስ)፣ ስንታየሁ ክፍሌ (አሙቅልኝ)፣ ይበለጥ ግዛው (ወይራው)፣ አቢይ ሳህሌ (መሮ)፣ አሰፋ ተገኝ (ባሻ)፣ አይቸው ሽመልስ (የገሊላ ሰው)፣ መርድ አባተ፣ መስፍን ጋሻው፣ ሀብታሙ ካሣዬ፣ አለማየሁ ጌታቸው፣ ሀና አሰፋና ብሩክታዊት ፋንታሁን ለቡሄ ጭፈራ ተነሱ፡፡ ሙዳይ በጎ አድራጎት ማህበር ሚኒባስ መኪና አቀረበ። የአካባቢው ወጣቶች፤ ኮሜዲያኑ ሄደው ቡሄ የሚጨፍሩባቸውን ግለሰብና ተቋማት መርጦ የመምራት ኃላፊነት ወሰዱ፡፡
ከኮተቤ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ሁለተኛ በር የጀመረው የኮሜዲያኑ የቡሄ ጭፈራ፣ወደ ኮተቤ መሳለሚያ አቅንቶ፣ ካራ በመድረስ በጤና ጣቢያዎች፣ ሆቴሎች፣ ቡና ቡቶች …. ለ3 ሰዓት ያህል ከተከናወነ በኋላ ወደ ሙዳይ በጎ አድራጎት ማህበር ግቢ ሲመለስ 10ሺ 345 ብር አሰባስቦ ነበር፡፡
ኮሜዲያኑ በቡሄ ጭፈራው ከሰበሰቡት ገንዘብ በላይ ለበጎ አድራጎት ማህበሩ ያደረጉት የማስተዋወቅ ሥራ ላቅ ያለ እንደነበር ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ ከቡሄው ጭፈራ በኋላ በሙዳይ በጎ አድራጎት ማህበር ግቢ ችቦ የማብራት ሥነ ስርዓት ተከናውኗል፡፡ ኮሜዲያኑ እግረመንገዳቸውን የግቢውን ተማሪዎች ለማዝናናትም ሙከራ አድርገዋል፡፡
ለአጭር ሰዓት በቆየው የውይይት መድረክም ኮሜዲያኑ በቁጭት ያነሱት ነገር ነበር፡፡ ጊዜ ተወስዶ ቢታሰብበትና ተዘጋጅተውበት ቢሆን ኖሮ፤ ብዙ ባለሙያዎችን በማሳተፍና በማስተባበር ትልቅ ሥራ መስራት ይቻል እንደነበር ገልፀዋል፡፡ በሙዳይ በጎ አድራጎት ማህበር ግቢ ውስጥ በበጎ ፈቃደኝነት የተለያዩ ሥራዎችን የሚያከናውኑ ወጣቶች ያመነጩት ሀሳብ ለኮሜዲያኑ አቀረቡ፡፡ ጉዳዩ መርካቶ ውስጥ በተመረጡ ቦታዎች ጫማ በመጥረግ ማህበሩን በማስተዋወቅ ረጂዎችን የመመልመል ተግባር ለመፈፀም ነው ያሰቡት። ኮሜዲያኑ በእቅዱ ለመሳተፍ ፈቃደኛ መሆናቸውን ገልፀዋል። “ችግርንም ጫማንም እንጠርጋለን” በሚል ቃል የሚካሄደው ፕሮግራም፤ ከጥቂት ሣምንታት በኋላ የሚጀመር ሲሆን ከተለያዩ አካላት የተውጣጡ አባላት ያለበት ኮሚቴም ተዋቅሯል፡፡
ስለሙዳይ በጎ አድራጎት ማህበር አመሰራረትና እያከናወነ ስላለው ተግባራት የሚተርክ የ15 ደቂቃ ዶክመንተሪ ላይ እንደሚታየው፤ የበጐ አድራጐት ማህበሩን በስሟ የመሰረተችው ወ/ሮ ሙዳይ ምትኩ ትባላለች፡፡ ማህበሩ ለሕፃናት፣ ሴቶችና እናቶች ድጋፍ የሚያደርግ ሲሆን በመጀመሪያ የተከፈተው በትምሀርት ቤትነት ነበር፡፡ በ1993 ዓ.ም የተቋቋመው “ፍሬሽ ኤንድ ግሪን ትምህርት ቤት” በክፍያ ተማሪዎችን ተቀብሎ ማስተማር ጀመረ፡፡ የሚያስተምር ሲሆን
ከፍለው መማር የማይችሉ ተማሪዎችን መርዳት የጀመረው በምሥረታው ማግስት ነበር። በነፃ የሚማሩት ልጆች ቁጥር እየበረከተ ሲመጣ ልጆቻቸውን ከፍለው የሚያስተምሩ ወላጆች ቅሬታ ማቅረብ ጀመሩ፡፡ ችግሩን ለመፍታትም መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ ተቋቋመ፡፡ ለወ/ሮ ሙዳይ የቀረበላት ጥያቄ ከሁለት አንዱን ምረጪ የሚል ነበር፡፡ ቢዝነሱ ይሻልሻል ወይስ በዕርዳታው ተግባር መሰማራት? ተባለች፡፡
“ችግረኛ ልጆችን መበተን አላስቻለኝም” የምትለው ወ/ሮ ሙዳይ፣ ሰብአዊነት ወደሚጠይቀው ተግባር ተሰማራች፡፡ ሙዳይ የበጎ አድራጎት ማህበርን በመመሥረት ለህፃናት ትምህርት፣ ምግብና ማደሪያ፤ ለወላጆቻቸውና ለተለያዩ ችግረኛ ሴቶች ደግሞ ስራ ፈጥራ የአቅሟን ማድረግ ከጀመረች 13 ዓመታትን አስቆጥራለች፡፡
160 ችግረኛ ልጆችን በመርዳት የጀመረው የበጎ አድራጎ ተግባር፤ አሁን በተለያዩ ደረጃ እየተረዱ ያሉት ሕፃናት ቁጥር 739 ደርሷል፡፡ ወ/ሮ ሙዳይ ምትኩ ይህንን የበጎ አድራጎት ተግባር የምታከናውነው በሁለት የገቢ ምንጭ ነው፡፡ የከብት እርባታ፣ የእንጉዳይና አትክልት ልማት ሥራዋ አንዱ የገቢ ምንጭ ሲሆን ለምትሰራው የበጎ አድራጎት ተግባር አቅማቸው በፈቀደ መጠን የተለያየ እርዳታ የሚያደርጉላት ሰዎች እገዛ ሌላው ነው። እንዲያም ሆኖ ግን ከተረጂዎቹ ቁጥር ብዛትና ከስራው ስፋት አንፃር ችግሮቹ ሰፍተው ከአቅሟ በላይ እየሆነ መምጣቱን ትናገራለች፡፡
የበጎ አድራጎት ሥራው፤ በወር 60ሺህ ብር ገደማ ኪራይ በምትከፍልባቸው የግለሰብ ቤቶች ነው የምታከናውነው፡ በየዕለቱ አንድ ኩንታል ጤፍ ተፈጭቶ ቢጋገርም ለተረጂዎቹ የምግብ ፍላጎት በቂ ሆኖ ስላልተገኘ በቅርቡ እራት ማብላቱን ለመቀነስ መገደዷን ወ/ሮ ሙዳይ ምትኩ ገልፃለች፡፡ “ከእህል ነጋዴዎች፣ ወፍጮ ቤቶች፣ የተለያየ ሸቀጣ ሸቀጥ ነጋዴዎች … በአመኔታ በዱቤ የወሰድኩባቸው ዕዳ መከማቸት የገጠመኝ ችግር አንዱ ማሳያ ነው” ትላለች፤ ወጣቷ የበጎ አድራጎ ማህበር መሥራች፡፡
በሙዳይ በጎ አድራጎት ማህበር ግቢ እየኖሩ እርዳታ ከሚያገኙት መሐል አንዱ ህፃን የሱነህ አስራት ይባላል። የሕፃኑ ወላጆች ልጃቸው ማየትም፣ መስማትም፣ መናገርም ሆነ መቆም እንደማይችል የተረዱት ከተወለደ ከ6 ወር በኋላ ነበር፡፡ የሱነህ ከወላጆቹ ተገቢውን እርዳታ ማግኘት አለመቻሉን የሰማችው ወ/ሮ ሙዳይ፤ ህፃኑን ወደ ማዕከሉ አምጥታ የተሻለ እርዳታ እንዲያገኝ አደረገች፡፡
አሁን የ6 ዓመት ልጅ የሆነው የሱነህ አስራት፤ ለብቻው ሞግዚት ተመድለት እንክብካቤ ይደረግለታል። ትንሽ ትንሽ መቆም ጀምሯል፡፡ የመስማት፣ የመናገርና የማየት ተስፋ እንዳለውም በሐኪሞች ተረጋግጧል። የችግሩ ዋነኛው ምክንያት ጭንቅላቱ ውስጥ ያለ እጢ መሆኑ ታውቋል፡፡ ችግሩን ለመቅረፍ ኦፕራሲዮን ከመሞከር ይልቅ በሂደት ለውጥ የሚያመጣ መድኃኒት እየተሰጠው መሆኑንና ከ4 ዓመት በኋላ ህፃን የሱነህ ዓይኖቹ ማየት እንደሚችሉና ችግሮቹ እንደሚቀረፉ በሐኪሞች ተነግሯቸው፤ በተስፋ እየተጠባበቁ መሆናቸውን ለህፃኑ የተመደበችለት ሞግዚት ትገልፃለች።
የቡሄና የአሸንዳ በዓልን ምክንያት በማድረግ፤ የበጎ አድራጎት ማህበሩን ተግባራት ለህብረተሰቡ ለማስተዋወቅ የታሰበውን ፕሮግራም ለመመልከት በቦታው የተገኙት የኮሜዲያን ማህበር አባላት ምንም ባልተዘጋጁበት ሁኔታ የፈጠሩት ገቢ የማሰባሰብ፣ ለአካባቢው ህብረተሰብ ግንዛቤ የማስጨበጥና የበጎ አድራጎት ማህበሩን አባላት የማዝናናት እንቅስቃሴ ድንቅ ነበር፡፡ “ችግርንም ጫማንም እንጠርጋለን” በሚል ሊካሄድ በታቀደው ፕሮጀክት የተሻለ ነገር እንሰራለን ብለዋል - ኮሜዲያኑ፡፡

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ለጿሚዎች እንኳን ጾመ ልጓሙን ፈታላችሁ፡፡
በልክ ይበላማ!
እኔ የምለው…. በፍልሰታ ጾም መያዣ ዋዜማ  አዲስ አበባ የእውነትም የጉድ አገር ሆና ነበር። የምር እኮ… በተለይ ወደ ማታ ላይ ትልቅም ሆነ አነስ ያለ ምግብ ቤት ገብታችሁ ዘና ብሎ መብላት ብሎ ነገር የለም፡፡ ገና የመጨረሻዋን ጉርሻ ከሳህን አንስታችሁ ሳትጨርሱ አሳላፊ መጥቶ ይወስደዋል። ቦታ እስኪለቀቅለት የሚጠብቅ ሰው መአት ነበራ! የታወቁ ክትፎ ቤቶች ገና አንድ ሰዓት ሳይሞላ “ክትፎ አለቀ…!” የተባለበት ቀን ነበር፡፡
የምር ግን…አለ አይደል…ትርጉም ያላቸው በዓላት ትርጉማቸውን ሲያጡ የሆነ የሚበላሽባችሁ ነገር አለ፡፡
ይቺን ስሙኝማ…አዲስ አስተናጋጅ ነች አሉ። ብዙም ስለ ምግብ ቤት አታውቅም፡፡ እና የሆነ ተመጋቢ ይገባል፡፡
“ጌታዬ ምን ልታዘዝ?” ትላለች፡፡ እሱም..
“መጀመሪያ ሜኑውን ላንብበው…” ሲላት ምን ብትለው ጥሩ ነው…
“ጌታዬ ለማንበብ ከፈለጉ ወደ ላይብረሪ ቢሄዱ ጥሩ ነው…” ብላው አረፈች፡፡
ስሙኝማ…የአስተናጋጅ ነገር ካነሳን አይቀር፣ ነገሬ ብላችሁ ከሆነ ብዙ ምግብ ቤቶች አሳላፊዋ የ‘በያይነቱ’ን ትሪ አንዴ ከወረወረችላችሁ በኋላ ብቅ ማለት ዘበት ነው… በእሷ ቦታ የበቀደሞቹን የአማሪካን ውሾች የሚያክል ድመት ስምንት ጊዜ ይመላለሳል፡፡
የምር ግን… በመቶ ‘ፐርሰንት’ የባንክ ብድር ምግብ ቤት ልከፍት ካሰብኩ የትም አፈላልጌ ነው የማገኛት፡፡ አሀ…ምን የሚያካክሉት ካፌዎች እንኳን ልክ ‘ባለማጨስዎ እናመሰግናለን’ እንደሚባለው ‘ጋዜጣ ባለማንበብዎ እናመሰግናለን’ ብለው እየለጠፉ አይደል! ስለዚህ ገብቶ “ምንቸት አብሽ…” “ቋንጧ ፍርፍር…” እያለ ይዘዝ እንጂ “ሜኑ ላንብብ…” ቅብጥርስዮ የሚባለው…የእኔ ምግብ ቤት የንባብ ባህል ማዳበሪያ ነው፡፡  ቂ…ቂ…ቂ…
የምር ግን…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…የምግብ ቤት ባለቤቶቹ ችግር ቢገባኝም  “ጋዜጣ ማንበብ ክልክል ነው…”  “ከእኩል ሰዓት በላይ ማንበብ ክልክል ነው…” ምናምን የሚሉ ማስታወቂያዎች ስታነቡ አታዝኑም!  ለነገሩማ… አንዳንዱ እኮ አንዲት ስኒ ሻይ ይዞ ከቁርስ እስከ ምሳ ሰዓት ተቀምጦ (የ‘ጨዋ’ ቃል ለመጠቀም ያህል!) የሚውለውን ስታዩ ባለቤቶቹስ ምን ያድርጉ ያሰኛችኋል።
ስሙኝማ…የበዓል ነገር ካነሳን አይቀር…‘የበዓል መንፈሳችን’… አለ አይደል… “ከአፍሪካ አንደኛ፣ ከዓለምም አንደኛ” ምናምን ነገር ቢባል አይገርምም።
ዘንድሮ እኮ የአብዛኞቹ በዓላት ‘ዋዜማ’ የሚጀምረው ገና ሁለት ሳምንትና ከዛ በላይ ሲቀረው እየሆነ ነው፡፡ ልክ ነዋ…ይኸው “እንኳን ለአዲሱ ዓመት አደረሰህ/ሽ…” መባባል ጀምረን የለ!
ስሙኝማ…ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…በዓል ሲቃረብ በማስታወቂያውም፣ በ‘አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች’ ነገርዬውም ‘ታዋቂ ሰዎች’ ቴሌቪዥናችንን መሙላታቸው አይቀርም፡፡ እንኳንም ‘ታዋቂ’ ሆኑልንማ!
እኔ የምለው…የ‘ታዋቂነትን’ ነገር ካነሳን አይቀር…እዚህ አገር እኮ የራስን ታሪክ ‘ለመከለስ’… አለ አይደል… ‘ታዋቂ’ መሆንን የመሰለ ነገር የለም፡፡ ልክ ነዋ…ታሪካችሁን በፈለጋችሁ መንገድ ለመተርክ ‘መብቱ’ አላችኋ!
“ገና የኔታ ዘንድ ሀ ሁ መቁጠር ሳልጀምር ጀምሮ ነው ኖቤል ሽልማትን የማግኘት ምኞት ያደረብኝ…” ሲባል “ወራጅ አለ…” “የረገጣዎች ሁሉ እናት!” “ለምን ይዋሻል!” ምናምን ብሎ ነገር የለም፡፡ ይልቁንም የእኔ ቢጤው ጥያቄ አቅራቢ… “ገና ከልጅነቱ ጀምሮ ኖቤል ሽልማትን በማሸነፍ ፍቅር የተነደፈ…” ምናምን ብሎ ያሳምረዋል፡፡
‘ታዋቂው’ የፊልም ተዋናይ…እንዴት ‘የፊልም ፍቅር’ እንዳደረበት ሲናገር…“ልጅ እያለን አባታችን ሁልጊዜ የዲቪዲ ፊልም እየያዘልን ይመጣ ነበር…” ምናምን ነገር ይላል፡፡
አባትየው እኮ አይደለም የዲቪዲ ፊልም ይዘው ሊመጡ…ቴሌቪዥን ከጥቁርና ነጭ ወደ ቀለም መለወጡን ሳያውቁ ነው ከዚህ ዓለም የተሰናበቱት፡፡
ስሙኝማ…የዚህ አገር የ‘ታዋቂነት’ ነገር ምን ደስ ይልሀል አትሉኝም… አብዛኞቹ ‘ታዋቂ’ ሰዎች ታዋቂ እንደሚሆኑ የሚያውቁት ገና የተወለዱ ዕለት ጀምሮ ይመስላል፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
“ልጅ እያለሁ ጀምሮ አንጀሊና ጆሊን መሆን እመኝ ነበር፡፡” ይሄኔ እኮ… አለ አይደል…እሷ ‘ልጅ እያለች’ አንጀሊና ጆሊ ትወና አልጀመረችም!
‘ታዋቂው’ ፖለቲከኛ (‘ታዋቂ ፖለቲከኛ’ ምን ማለት ነው!) ነው የሚባለውም…“ከልጅነቴ ጀምሮ የሰው ጥቃት ማየት አልወድም፡፡ ማንም ሰው ሲጠቃ ሲያይ ቀድሜ የምገባው እኔ ነኝ…” ይላል፡፡ ከትንሹም ከትልቁም እየተጋጨ ወላጆቹ በየሦስት ቀኑ ቀበሌ ይጠሩ ነበር፡፡ እናላችሁ…ታዋቂ መሆን አሪፍነቱ…ባዮግራፊን ‘ኤዲት’ ማድረግ ይቻላል፡፡
ስሙኝማ…ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…በአሁኑ ጊዜ “ሀብት ከማግኘቴ በፊት ሳምቡሳ እሸጥ ነበር…” ምናምን የሚሉ ሰዎች መሰማት ናፍቆናል፡፡ የምር…ልክ ፈረንጆቹ እንደሚሉት፤ ‘አፉ ውስጥ የብር ማንኪያ ጎርሶ’ የተወለደ ይመስል…“ይገርምሀል ነፍስ ከማወቄ በፊት እንኳን የቢዝነስ ችሎታው ነበረኝ…” ይባላል፡፡
‘ታዋቂው’ የሆቴል ቤት ባለቤትም…“ገና ልጅ እያለን ሁልጊዜ ትልቅ ሆቴል እንገባ ስለነበር በሆቴል ሥራ የመሰማራት ሀሳቡ ነበረኝ…” ይላል፡፡ እሱዬው ልጅ እያለ እኮ አይደለም ትልቅ ሆቴል…ነስሩ ፓስቲ ቤት የገባበት ጊዜ እንኳን በጣት የሚቆጠር ነው፡፡ ልክ ነዋ…ታዲያ እንዲህ አይነት ‘ኤዲቲንግ’ አለ እንዴ!
“አበባየሁ ወይ…” ከሚጨፍሩ ልጆች ጋር ታይተሻል እየተባለች ‘ቀሚስ ተገልቦ’ ስትጠበጠብ የነበረችው ‘ታዋቂ’ ዘፋኝ… “ልጅ እያለሁ ጀምሮ ድምጻዊ እንድሆን ቤተሰቦቼ ከፍተኛ እገዛ አድርገውልኛል…” ማለት ነው፡፡
እናላችሁ…‘ታዋቂ’ ሆናችሁ፣ ወይንም “ታዋቂ ነኝ ብላችሁ አስባችሁ…” ለቃለ መጠይቅ ከቀረባችሁ…ብልጥ መሆን ነው፡፡ አንድ ሲንግል ለቆ… “የዘፈን ችሎታ እንዳለህ ያወቅኸው መቼ ነው?” ሲባል… “ገና ስወለድ ለቅሶዬ በዜማ ነበር አሉ…” ማለት ነው ልክ ነዋ፡፡
“የስነጽሁፍ ፍቅር ያደረብህ መቼ ነው?” ሲባል… አለ አይደል… “ገና አንድ ዓመት እንኳን ሳይሞላኝ ፍቅር እስከ መቃብር መጽሐፉን ይዤ አልለቅም ብዬ አለቅስ ነበር…” ማለት ነው፡፡  
ዘፋኝ ነው አሉ፡፡ እና የሆነች ከተማ ኮንሰርት ለማቅረብ ይሄዳል፡፡ ክፍያውን ከፍ ለማድረግም ለአዘጋጁ ምን ይለዋል…“እዚሀ ከተማ ሁሉም ሰው ያውቀኛል፡፡”
ታዲያላችሁ…ኮንሰርቱ ላይ ሦስት ሰዎች ብቻ ይመጣሉ፡፡ አዘጋጁም ይናደድና…
“ምን አይነት ውሸታም ነህ!” ይለዋል፡፡
“ምን አደረግሁ?”
“ሰዉ ሁሉ ያውቀኛል አላልክም እንዴ!  ሦስት ሰው ብቻ ነው እኮ የመጣው…” ሲለው ታዋቂው ድምጻዊ ምን ቢል ጥሩ ነው…
“የመጡት የማያውቁኝ ሦስት ሰዎች ናቸው፡፡ የሚያውቁኝማ ያውቁኛል…” ብሎ ቁጭ፡፡
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ነገራችን ሁሉ “እንኳን በዓል መጥቶ እንዲሁም ብላ፣ ብላ… ጠጣ፣ ጠጣ ይለኛል…” አይነት ነገር ሆኖ የለ…በልክ ቢሆን አሪፍ ነው፡፡
እኔ የምለው… ከእኔ ቢጤ ‘ባዶ ኪስ፣ ሙሉ ምላስ’ ወዳጆቼ ጋር ስንገናኝ ሁል ጊዜ ከአፋችን የማይጠፋው ዓረፍተ ነገር ምን መሰላችሁ… “ሰዉ ገንዘብ ከየት ነው የሚያመጣው?” የሚል ነው። ያስብላላ! ለቲማቲምና ሽንኩርት የሠላሳና አርባ ብር ተጨማሪ ወጪ ሲጠየቅ… “የዘይት ጉድጓድ አለኝ መሰለሽ!” ብሎ ከሚስቱ ጋር የኑክሌር ጦርነት ለመጀመር ምንም የማይቀረው አባወራ፣ ከረፋድ ጀምሮ ‘ሲገለብጠው’ ስታዩ “ሰዉ ገንዘብ ከየት ነው የሚያመጣው?” የማያስብላችሁሳ!
ሰውየው ምን አለ አሉ መሰላችሁ… “የኪስ ቦርሳዬ እንደ ሽንኩርት ነው፣ በከፈትኩት ቁጥር እንባዬ ይመጣል።”
እናማ…እንዲህ በሚባልበት ዘመን…አለ አይደል… የቤቱ መሶብ ባዶ ሆኖ በየክትፎ ቤቱ ‘ቦታ እስኪለቀቅ’ ሰልፍ የሚያዝበትን ዘመን ስታዩ፣ የሆነ ልክ ያልሆነ ነገር እንዳለ ይታያችኋል፡፡ በገንዘብ ቦርሳችን ስጥ ብሩን ብቻ ሳይሆን አርቆ ማስተዋልን የሚያስገባልን ተአምሩን ይላክልን፡፡
“የኪስ ቦርሳዬ እንደ ሽንኩርት ነው…” ከማለት ይሰውረንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

የአባ ባሕርይ መዝሙር /3/ በግጥም መልክ በግዕዝ ቋንቋ የፃፉት የሚከተለው ምሣሌ ይገኝበታል፡፡ እንዳመቸ አቅርበነዋል፡፡
በአንድ ዘመን እንዲህ ሆነ፡፡ አንድ ሰው በመንገድ እየሄደ ሳለ፣ በድንገት ከየት መጣ ሳይባል አንድ አውራሪስ ከተፍ አለበት፡፡ ሰውዬው እግሬ አውጪኝ ብሎ ፈፋውን ጉድባውን እየዘለለ፣ ጫካውን እያቋረጠ መጭ አለ፡፡ ፍርሃቱ የትየለሌ ሆነ፡፡ ነብሱን ሳያውቅ ሸሸ፡፡ በመጨረሻ ገደል ገጠመውና ወደ ገደሉ ሲወድቅ አንድ የዛፍ ቅርንጫፍ ፈፋውን ታኮ ተዘርግቶ ኖሮ፤ ያን ሲያይ ሰውዬው አፈፍ አድርጐ ተንጠለጠለበት፡፡ እዚያው ተንጠልጥሎም ሳለ፤ ከጐኑ በኩል አራት እባቦች እየተሳቡ ሲመጡ አየ፡፡ ይብስ ብሎም ከበታቹ አንድ ዘንዶ አየ፡፡ ያ ዘንዶ ሰውዬውን ለመዋጥ አፉን ከፍቶ ወደ እሱ እየተንጠራራ ይጠብቀዋል፡፡
ቀን ያመጣው አይቀሬ ነውና ሁለት ጥቁርና ነጭ አይጦች ደግሞ፤ ሰውዬው የተንጠለጠለበትን የዛፍ ቅርንጫፍ ተጐምዶ እንዲወድቅ እየገዘገዙ የበኩላቸውን እኩይ ተግባር እየፈፀሙ ይገኛሉ፡፡ እኒህንም አየ፡፡
በዚህ ሁሉ መሃል፣ ሰውዬው በፍርሃትና በጭንቀት ተውጦ እያለ፣ ከዚያ ዛፍ ቅርንጫፍ ላይ የሚንጠፈጠፍ የማር ወለላ አየ፡፡ ሰውዬው አፉን ከፈተና ማሩ ወደ አፉ ይፈስለት ዘንድ ጠበቀ፡፡ የማር ወለላው ጥቂት በጥቂት ፈሰሰለት፡፡
ከቶውንም በምን ዘዴና ብልሃት ላመልጣቸው እችላለሁ ያላቸውን ፍርሃቶች፤ ከባዶቹን የእባብ፣ የዘንዶና የአይጥ ፈተናዎች በምን መንገድ አልፋቸዋለሁ? የሚሉትን ጭንቀቶች፤ በወለላው ጣዕም ምክንያት ለጥቂት ጊዜ ሊረሳቸው ቻለ፡፡
                                                   *   *   *
የሰው ልጅ እጅግ አስከፊ በሆነ መከራና ጣጣ አረንቋ ውስጥ ወድቆ እንኳ አንዳች ፋታ የሚያገኝባትን ቅንጣት ቅፅበት ይፈልጋታል፡፡ በእሷም ረክቶ ህይወቱን የሚታደግባትን ተስፋ ይጠነስሳል፡፡ ገደል የከተተውን አውራሪስ መሸሹ እኩይ ዕጣው ነው! ሙሉ በሙሉ ገደል ገብቶ እንዳይንኮታኮት ያ ቅርንጫፍ ተዘርግቶ መጠበቁ ሰናይ ዕጣው ነው፡፡ ከዚህ ዙሪያ ደግሞ እባብና ዘንዶ አሰፍስፈው መንጠራራታቸው፣ ለሰውዬው የታዘዙ እኩይ ዕጣዎች ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ ጠብታዋ ወለላ ማርም የሰውዬው ሰናይ ዕጣ ናቸው! መከራዎቻችን የተስፋ ዕልባት አላቸው፡፡ በብዙ ድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ነጥብ ብርሃን የማየት ችሎታ መኖር መታደል ነው!
አያሌ ውጣ - ውረዶችን ባየንባት አገራችን፤
“ኧረ እናንተ ሰዎች ተውኝ እባካችሁ
እንኳን የመሶቡን የጄን ተውኩላችሁ”
…ስንል ኖረናል፡፡ ለማን ነው የምንተወው? ለምንድን ነው የምንተወው? እስከመቼስ የምንተወው? የሚሉትን ጥያቄዎች አላነሳንም፡፡ በዚህ ውስጥ መታሰብ ያለባቸውን ኃላፊነታችንን የመወጣትና መብታችንን የማስከበር ፍሬ - ጉዳዮች ምን ያህል አስበንባቸዋል? በምን ያህል ዕቅድና የረዥም መንገድ ትግበራስ ውጤታማ እንደምንሆን እርግጠኞች ነን? ማለት የአባት ነው፡፡
ተጨባጭ ችግሮቻችንን በተጨባጭ መንገድ መፍታት አለመቻል አንዱ ተጨባጭ ችግራችን ነው፡፡ በሀሳብ አንደጋገፍም፡፡ ሀሳብ ካቀረብን ስለችግር እንጂ ስለመፍትሄ አይደለም፡፡ ስለሆነም በችግራችን ላይ ሌላ ችግር ጨምረን ነው የምንለያየው፡፡
የኮሚቴ መብዛት ችግር አለ ተብሎ፣ ያን የሚፈታ ኮሚቴ እናቋቁም ብለው ተለያዩ እንደተባለው  ነው፡፡ አንዱ መሰረታዊ ዕጣችን ስለጊዜ ያለን አስተሳስብ ነው፡፡ ሊቀ-ጠበብት አክሊለ ብርሃን የደረሱትን ማህሌት ልብ እንበል፡-
“በሰላማ ጊዜ የረጋ ወተት
ተንጦ ተንጦ ቅቤው ወጣለት”
ጊዜ የወሰደ ሰው አንድ ቀን ቅቤው ይወጣለታል ነው ነገሩ፡፡ ጊዜን አርቀን ለማሰብ ግን የአዕምሮም የልቡናም አቅም የለንም፡፡ (ለምሳሌ የሃያ ዓመት ዕቅድ አይገባንም፡፡)
ከቀደምት ዘመናት ጀምሮ በአገራችን ብዙ አጋጣሚዎችን አጥተናል፡፡ በተለይ ቀለም የቀመሰው ክፍል ብዙ ዕድሎችን አጥቷል፡፡ አንድም አንፃር በማብዛት፣ አንድም ከሥርዓቱ ጋር አብሮ የመሥራት ባህል ስለሌለው፡፡
“አገራችን የዕድል ሳይሆን የታጡ - ዕድሎች አገር ናት” ይላል አንድ ፈላስፋ (A land of missed opportunities not of opportunities) የእኛም ምሁራን እንዲሁ ቢሉ እንዴት መልካም ነበር! ዶክተር ጌታቸው ኃይሌ ከፃፉት ውስጥ “ጌታ ዲነግዴ የሳምንት ገበያ ሲደርስ ከከብቶቻቸው አንዱን በሬ ለመሸጥ ገበያ ይወስዳሉ፡፡ ግን አንዳንድ ጊዜ ገበያ እስኪፈታ እዚያው ውለው በሬውን ሳይሸጡት ይቀሩና መልሰው ያመጡታል፡፡ አባቴ፤ “ጌታ ምነው በሬውን መለሱት? ገዢ አጡ እንዴ?” ሲላቸው፤ “የለም ልጄ ገዢስ ሞልቶ ነበር፤ ግን ስጠይቃቸው፤ በቀዬው ለበሬዬ የሚበቃ የመስኖ ሣር ያለው አንድም ሰው አላገኘሁም፡፡ ለእነሱ ሸጬ በሬዬን ረሀብ ላይ እንዳልጥለው ብዬ መልሼ አመጣሁት” ይሉታል… የሚል ይገኝበታል፡፡ ይህንንም በምግብ ራስን መቻል ከሚለው የዛሬ ትግላችን ጋር አዛምዶ ማየት ደግ ነው! በሬው ተሸጦ የሚበላው እንዳያጣ የሚታሰብበትም ዘመን ነበር - ያኔ፡፡
በተደጋጋሚ ከሚነሱት የምሁር አምባ ችግሮች ወሳኙ፤ “ጠባብነትና ትምህክተኝነት የምሁሩ አባዜዎች መሆናቸውን አለመርሳት ነው!” የሚለው ነው፡፡ በሁለቱም ፅንፍ የተቸከልን ብዙ ምሁራን አለን! አምላክ ደጉን ያምጣልን!!
አበሻ “ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኸ” ይለናል፡፡ ችግሮቻችን መፍትሄ ሳያገኙ ሰንብተው ካንሠር አከል (Cancerite) ከሆኑ በኋላ ብንጮህላቸው ከንቱ መባዘን ነው፡፡ “ቀድሞ ነበር እንጂ መጥኖ መደቆስ አሁን ምን ያደርጋል ድስት ጥዶ ማልቀስ” የተባለውን ማጤን ነው፡፡
አገር እንደ ፅጌረዳ አበባ ብንመስላት፤ “ፅጌረዳዋ ከደረቀች በኋላ፣ ጎርፍ የሆነ ዝናብ ምን ይበጅ?!” የሚለው ይገባናል፡፡ ቀድመን እንዘጋጅ!!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

    አቃቤ ህግ ይግባኝ እጠይቃለሁ ብሏል
    ከአንድ አመት በፊት በሽብር ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ከዋሉት 10 ተከሳሾች መካከል  የቀድሞ የአንድነት የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሀብታሙ አያሌውን ጨምሮ አራት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና አንድ ሌላ ግለሰብ በቀረበባቸው ክስ ላይ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ፍ/ቤቱ ከትናንት በስቲያ በይኗል፡፡ ቀሪዎቹን 5 ተከሳሾች ይከላከሉ ብሏል - ፍ/ቤቱ፡፡ አቃቤ ህግ ይግባኝ እጠይቃለሁ ብሏል፡፡
ፍ/ቤቱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮቹን፡- ሀብታሙ አያሌው፣ የሸዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታና ዳንኤል ሺበሺ እንዲሁም አብርሃም ሰለሞን የተባለውን ግለሰብ ነው በነፃ ያሰናበተው፡፡ ዘላለም ወ/አገኘሁ፣ ዮናታን ወልዴ፣ ሰለሞን ግርማ፣ ባህሩ ደጉና ተስፋዬ ተፈሪ የተባሉት ተከሳሾች ደግሞ ተከላከሉ ተብለዋል፡፡
አቃቤ ህግ፤ ግለሰቦቹ ከ2000 ጀምሮ ግንቦት 7 ከተባለ የሽብርተኛ ድርጅት ጋር ግንኙነት በመፍጠር፣ በተለያዩ ማህበራዊ ድረገፆች መረጃ በመለዋወጥ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ በአረቡ ዓለም የተከሰተውን አመፅ ለመተግበር የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ማድረጋቸውንና ከሽብር ድርጅቱ የሚላክላቸውን ገንዘብ እስከመቀበል መድረሳቸውን በመጥቀስ ነው በአራት የሽብር ወንጀሎች ክስ የመሰረተባቸው፡፡የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበረው አቶ ሀብታሙ አያሌው ላይ አቃቤ ህግ ያቀረባቸው ማስረጃዎች፣ አንድ ሳምሰንግ
ሞባይል ስልክና ከብሄራዊ መረጃና ደህንነት ተገኙ የተባሉ ተከሳሹ በተለያዩ ስብሰባዎች ላይ ያስተላለፋቸው መልዕክቶችና የስልክ ልውውጦች ሲሆኑ የአቃቤ ህግ ምስክሩም በፍተሻ ወቅት ሳምሰንግ ሞባይል በቤቱ እንደተገኘና በስልኩ ውስጥ ምን እንዳለ እንደማያውቅ ለፍ/ቤት አስረድቷል፡፡ ፍ/ቤቱም ማስረጃዎቹንና ምስክሩን መርምሮ በሰጠው ብይን፤ ግለሰቡ ሳምሰንግ ሞባይል ብቻ መያዙ ሽብርተኛ አያስብልም ብሏል፡፡
በማስረጃነት የቀረቡትን ሰነዶችም የመረመረው ፍ/ቤቱ፤ ንግግር አድርጓል በሚል የቀረቡት ማስረጃዎች የሚያስረዱት የአንድነት ድርጅት የመረጃ ኃላፊ መሆኑን ብቻ ነው በማለት ክሱ በሰውና በሰነድ ማስረጃ ያልተደገፈ በመሆኑ በነፃ እንዲሰናበት በይኗል፡፡ ሌላው ተከሳሽ የአንድነት ፓርቲ የድርጅት ጉዳይ ም/ኃላፊ ዳንኤል ሺበሺም ሁለት ሳምሰንግ ሞባይል እንደተገኘበትና በሞባይሉ ውስጥ ምን እንዳለ አለማየታቸውን የአቃቤ ህግ ምስክሮች ማስረዳታቸውን የጠቀሰው ፍ/ቤቱ፤ ከብሔራዊ ደህንነት መረጃ የተገኘው ሰነድም
ክሱን በበቂ የሚያስረዳ አይደለም ሲል ግለሰቡን በነፃ አሰናብቷል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አቶ የሸዋስ አሰፋና የአረና ፓርቲ አመራር አቶ አብርሃ ደስታም በተመሳሳይ ሁኔታ በነፃ የተሰናበቱ ሲሆን፤ ከፖለቲካ ፓርቲ አመራሮቹ በተጨማሪ ሌላው ተከሳሽ አብርሃም ሰለሞንንም ፍ/ቤቱ በነፃ አሰናብቷል፡፡ በነፃ ከተሰናበቱት ተከሳሾች መካከል ሀብታሙ አያሌውና አብርሃም ሰለሞን በሌላ ጉዳይ የማይፈለጉ ከሆነ ከሐሙስ ጀምሮ ከማረሚያ ቤት እንዲለቀቁ ፍ/ቤቱ ያዘዘ ሲሆን የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታና ዳንኤል ሺበሺ ከዚህ ቀደም ፍ/ቤት በመዳፈር  እስከ 1 ዓመት ከ4 ወር በሚደርስ  እስራት የተቀጡ በመሆኑ ቅጣታቸውን ሲጨርሱ እንዲፈቱ በይኗል፡፡ ተከላከሉ በተባሉት 5 ተከሳሾች ላይ ፍ/ቤት ምስክሮቻቸውን ለመስማት ለህዳር 13 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል፡፡ የፍርድ ቤቱን ብይን አስመልክቶ አስተያየታቸውን የሰጡት የሰማያዊ ፓርቲ ም/ፕሬዚዳንት አቶ ስለሺ ፈይሣ፤ የፓርቲያቸው አመራር
አባል አቶ የሺዋስን ጨምሮ ፖለቲከኞቹ ነፃ መባላቸው ተገቢ መሆኑን ጠቅሰው፣ “አስቀድሞም እነዚህ ሰዎች ሽብርተኞች አልነበሩም፤ በሰላማዊ ትግል የሚያምኑ ሰላማዊ ታጋዮች ናቸው” ብለዋል፡፡
በእነ የሸዋስ ላይ ምንም ማስረጃ አልተገኘም መባሉ የተፈረደባቸው ሌሎቹ እስረኞች ማስረጃ ተገኝቶባቸዋል ማለት እንዳልሆነ አቶ ስለሺ አክለው ተናግረዋል፡፡ በነፃ ከተሰናበቱት የአንድነት አመራሮች ጋር በአንድ ካቢኔ ውስጥ ሲሰሩ የነበሩት የፓርላማ አባሉ የተከበሩ አቶ ግርማ ሰይፉ በሰጡት
አስተያየት፤ በፍ/ቤቱ ውሳኔ ደስተኛ መሆናቸውን ጠቁመው፤ እንዲህ ያሉ የፍ/ቤት ውሳኔዎችን ማበረታታት እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡  መንግሥት በጀመረው መንገድ ሌሎች የህሊና እስረኞችንም መፍታት አለበት ብለዋል - አቶ ግርማ፡፡

Published in ዜና

.  የዘረኝነት ወረርሽኝ ለኢትዮጵያ አስፈሪ እንደሆነ ብዙዎች ይናገራሉ። እርስበርስ፣ “አንተ ነህ ዘረኛ”፣ “አንቺ ነሽ ዘረኛ” እያሉ ይወነጃጀላሉ። ብዙዎቹ የሚያቀርቧቸው አማራጮች ግን፣ በቅፅል ብቻ የሚለያዩ የዘረኝነት መልኮችን ነው።
.   ኢህአዴግ፣ ተቃዋሚዎቹን ያወግዛል - “የሁለት ተማሪዎችን ፀብ፣ የብሔረሰብ ፀብ አስመስለው ያራግባሉ” በማለት። ተጠያቂዎቹ፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከሆኑ፣ ስልጣን ላይ ከሃያ አመት በላይ የቆየ ፓርቲ፣ ይህን በሽታ ማቃለል ለምን አቃተው?
.   በርካታ ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ ኢህአዴግን ይኮንናሉ - “የብሄረሰብ ፖለቲካን አስፋፍቷል፤ የቀበሌ መታወቂያ ላይ ይመዘግባል” በማለት። ግን፣ ኢህአዴግ ስልጣን ባልያዘበት በአሜሪካ፣ በዳያስፖራ ፖለቲካና በፌስቡክስ ዓለም ለምን ዘረኝነት ገነነ?
.   በዚህ መሃል ግን፣ የዘረኝነት ወረርሽን ከአመት አመት እየተባባሰ፣ አገሪቱ እየተንሸራተተች ናት።    
   ምንም እንኳ፣ ኢትዮጵያ በብዙ አይነት የጥፋት ፈተናዎች ውስጥ፣ ህልውናዋን ሙሉ ለሙሉ ሳታጣ ያለፈች አገር ብትሆንም፣ የበርካታ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች ዝንባሌን ስትታዘቡ፣ የበርካታ ምሁራንና ዜጎች አዝማሚያ ስትመለከቱ... ሁሌም ባይሆን አንዳንዴ፣ የዚህች አገር ነገር፣ተስፋ ያስቆርጣል። ከአመት አመት፣ የዘረኝነት ወረርሽኙ እየባሰበት፣ አገሪቱ ወደለየለት የጥፋት አዘቅት እንዳትሰምጥ አትሰጉም? በእርግጥ፣ አልፎ አልፎ፣ የዘረኝነት በሽታው፣ ለአፍታ ጋብ ሲልለት... እሳቱም ትንሽ ሲበርድለት እያየን፣ የእፎይታና የተስፋ ስሜት እናገኛለን። ግን፣ እፎይታው ብዙም አይቆይም። እንደገና በሽታው ያገረሸበታል። ማገርሸት ብቻ አይደለም። ከእያንዳንዱ እፎይታ በኋላ፣ ወረርሽኙ ባገረሸ ቁጥር፣ ከቀድሞው እጅጉን ብሶበት እናገኘዋለን። ተስፋ አስቆራጩና አስፈሪው ነገር ደግሞ ምን መሰላችሁ? የዘረኝነት ወረርሽኙን ለማስቆም የሚያስችል፣ አስተማማኝ መላ ምን እንደሆነ በግልፅ ጎልቶ አለመታየቱ ነው። ዙሪያው ሁሉ በጨለማ የተዋጠ ጉዞ ይመስላል።
የዘረኝነት ወረርሽኝ፣ ተስፋ አስቆራጭና አስፈሪ የጨለማ ጉዞ የሚሆነው፤ ነገሩ ያን ያህል ውስብስብ ጉዳይ ስለሆነ አይደለም። ሰሞኑን ጠ/ሚ ኃይለማሪያም  ደሳለኝ፣ የተናገሩትን መጥቀስ ይቻላል። በተለይም፣ በዩኒቨርስቲዎች የሚታየው የዘረኝነት አስተሳሰብ አሳሳቢ መሆኑን በመጥቀስ ሲናገሩ እንዲህ ብለዋል።
አንድ የአማራ ተወላጅና አንድ የኦሮሞ ተወላጅ፣ ወይም አንድ የትግራይና አንድ የሶማሌ ተወላጅ ... በሆነ ምክንያት ቢጣሉና ቢደባደቡ፤ “አማራና ኦሮሞ ተደባደቡ”፣ “ትግሬና ሶማሌ ተጣሉ” ተብሎ ይራገባል። እንዲህ፣ የዘረኝነት አስተሳሰብ፣ በየቦታውና በየጊዜው መስፋፋቱ፣ በተለይም በዩኒቨርስቲዎች መባባሱ አሳሳቢ እንደሆነ የተናገሩት ጠ/ሚ ኃይለማሪያም፤ አንዴ ከእጃችን ካመለጠ፣ የጥፋት መዘዙ መመለሻ የለውም ብለዋል። ማብቂያ ወደሌለው የጥፋት እሳት የገቡ አገራት፣ ምንኛ እንደተንኮታኮቱ ማየት እንደሚቻልም ጠቅሰዋል - አቶ ኃይለማሪያም። ትክክል ብለዋል። “ታዲያ፣ ይሄ ከኢህአዴግ የብሄረሰብ አደረጃጀት ጋር እንዴት ይሄዳል?” የሚል ጥያቄ መነሳቱ አይቀርም።  አዎ አይሄድም። ነገር ግን፣ የዘኝነትን ምንነት የገለፁበት አነጋገር ትክክለኛ ነው።
የሁለት ሰዎች ፀብም ሆነ ወዳጅነት፣ ድብድብም ሆነ ጋብቻ፣ ዝርፊያም ሆነ ግብይት... በቃ የሁለት ሰዎች ድርጊትና ፍላጎት ነው። የሚወገዝ አልያም የሚደነቅ ከሆነም፣ አድናቆትና ውግዘቱ፣ ከእነዚሁ ሰዎች ውጭ መዝለል የለበትም። ማለትም... ነገርዬም፣ የዘር ፀብ ወይም የዘር ወዳጅነት አይደለም። የጎሳ ድብድብ ወይም የጎሳ ጋብቻ አይደለም - የሆኑ ሰዎች ናቸው የሚደባደቡት ወይም የሚጋቡት። የብሄረሰብ ዝርፊያ ወይም የብሄረሰብ ግብይት አይደለም - የሆኑ ሰዎች ናቸው የሚዘርፉት ወይም የሚገበያዩት።
የተደባዳቢዎቹ ወይም የተጋቢዎቹ ቁጥር፣ የዘራፊዎቹ ወይም የገበያተኞቹ ቁጥር... አስር፣ ከዚያም አልፎ መቶና ሁለት መቶ፣ ወይም እልፍና ሚሊዮን ቢሆን እንኳ፣ እውነታውን አይቀይረውም። “የዘር፣ የብሄር፣ የጎሳ” ጉዳይ አይደለም። ተፈፅሞ ሊሆን አይችልም። ለምን?
በቃ፣ የሰው ተፈጥሮ እንደዚያ አይደለም። የጋራ የሆነ (የብሄረሰብ ወይም የጎሳ) አንጎልና አእምሮ የለም። ኖሮም አያውቅም። እውቀትና አስተዋይነት፣ አልያም ጭፍን እምነትና ስሜታዊነት... በዘር አይወረስም። የጋራ እጅ እና አፍ የለም። የብሔረሰብ፣ የጋራ ረሃብና ጥም የለም። ለብሔረሰብ፣ “መጉረስ” እና “መጎንጨት” ብሎ ነገርም የለም። እያንዳንዱ ሰው፣ የተመገበውንና የጠጣውን ያህል ነው፤ የእያንዳንዱ ሰው ረሃብና ጥም የሚቃለለው። የብሔረሰብ ወይም የጎሳ፣ “የጋራ አካል” የለማ። ከሁሉም በላይ ግን፣ የጋራ አንጎል ወይም የጋራ አእምሮ የለም። ይህንን መካድ ነው፤ ዘረኝነት ማለት። ያን ያህል ውስብስብ ጉዳይ አይደለም።
ብዙ መራቀቅና ርቆ መጓዝም አያስፈልግም። በወንድማማቾች፣ በእህትማማቾችን ወይም በእህት ወንድሞች መካከል፣... የእውቀት፣ የአስተዋይነት፣ የዝንባሌ፣ የፍላጎት፣ የድርጊት ልዩነትን ማየት በቂ ነው። “እህቴ ታዋቂ ሃኪም ናት” የሚል ማስረጃ ብቻ በማቅረብ፣ ወንድሟ፣ የሃኪምነት ሙያንና ማዕርግን ማግኘት አለበት እንዴ? እንደ እህቱ መማርና ማጥናት ይቅርና፣ እግረመንገድ ስለ ሰውነት ክፍሎች ልታስረዳው ከሞከረች፣ ራስምታት የሚነሳበት ሰው፣ እንዴት ሃኪም ነኝ ይላል? አዎ፣ ይችላል - እውቀትና ሙያ፣ በዘር የሚተላለፍ ከሆነ።
በተቃራኒው፣ ወንድሟ የራሱን ሕይወት ቢያጠፋ ደግሞ አስቡት። “ሞትና ሕይወት የጋራ ስለሆነ፣ እህት ወንድሞቹንም እንቅበራቸው” እንላለን እንዴ? ማንነት የጋራ ከሆነ ግን፣ የግድ ነው።
“እህትሽ፣ ለትዳሯ ታማኝ አይደለችም” በሚል ሰበብ፣ ሚስቱን የሚፈታ ሙሽራንም አስቡት። “ቅድመ አያትህ፣ ቤተሰባቸውን ጥለው እንደጠፉ ሰምቻለሁ” ... በሚል ምክንያት፣ ከባሏ ጋር የምትፋታ ሙሽሪትስ? ተጠያቂነት በዘር የሚወረስ ከሆነ፤ ይሄም የግድ ነው።
ዘረኝነት፣ የዚህን ያህል የለየት እብደት ቢሆንም፣ በሩቅ በሩቅ ዝምድና ይቅርና፣ በአንድ ቤተሰብ ውስጥ እንኳ የማይሰራ ቢሆንም፣ የዘረኝነትን አባዜ በቀላሉ አሽቀንጥረን ለማስወገድ አልቻልንም። አስገራሚ ነገር ነው። ጭራሽ፣ በዝምድና የሚገናኙ መሆን አለመሆናቸው የማይታወቁ ሰዎችን (የአንድ ብሔረሰብ ተወላጆችን) በጅምላ እንፈርጃለን። ይሄም አልበቃም። ጭራሽ፣ ከመቶ ዓመት በፊት፣ ... ከአምስት መቶ ዓመት በፊት፣ ከሚሌኒዬም በፊት የነበረ ንጉስና አልጋ ወራሽ፣ ወይም ደጃዝማቾችና ፊታውራሪ፣ አልያም ሰባኪና ፀሃፊ፣ ሽፍታና ዘራፊ... እየጠቀስን፣ አሁን በሕይወት ያሉ ሰዎችን፣ የጥፋትና የበደል ወራሽ እንዲሆኑ በዘር እየፈርጅንና እያቧደንን፣ አገሩን ቀውጢ ስናደርግ ይታያችሁ? እብደቱ፣ በሽታውና ወረርሽኙ የዚህን ያህል ከፍቷል።
ተስፋ አስቆራጩ ነገር፣ ... የጥንት ሰዎችን ድርጊትና ንግግር እየጠቀሱ ዘረኝነትን ማራገብ፣ እንደ ክፉ እብደት ሳይሆን እንደ አዋቂነት ሲቆጠር ታያላችሁ። ደህና ጤናማ የሚባሉ ሰዎች እንኳ፣ “ይሄ ታሪክ እውነት ነው ወይስ ሃሰት?” እያሉ ከመጠየቅ ያለፈ ነገር አያደርጉም። ከአምስት መቶ አመት በፊት፣ “እውነትም፣ እገሊት እንደዚያ ተናግራ ቢሆን፣ እገሌም ያኔ እንዲያ የፈፀመው ድርጊት ቢኖር”... አሁን በሕይወት ካሉ ሰዎች ጋር ምን አገናኘው? በአምስት መቶ አመታት ርቀትና ከሃያ የትውልድ ሃረግ ቆጠራ በኋላ ይቅርና... ያኔ ከአጠገባቸው የነበሩ የቤተሰብ አባላት እንኳ፣ ተጠያቂ ወይም ተሸላሚ መሆን የለባቸውም - በእህታቸው ንግግር ወይም በወንድማቸው ድርጊት። በየፊናቸው የተናገሩትና ያደረጉት ነገር ካለ፣ እንደ የስራቸው እንመዝናቸዋለን እንጂ። ጭራሽ፣ የምዕተዓመት ታሪክ እየጠቀሱ፣ ሰዎችን በዘር ለማቧደን መሞከር ግን... በቃ ልዩ በሽታ ነው።
ለነገሩ፣ የምዕተ ዓመታት ታሪክ እየጠቀሱ፣ “የዘር ወዳጅነት፣ የብሄረሰብ መፈቃቀር...” ለመፍጠር መከራቸውን የሚያዩም አሉ። የዘር ጥላቻን ወይም የብሄረሰብ ፀብን መስበክ ዘረኝነት የመሆኑን ያህል፣ የዘር መፈቃቀርን ወይም የብሄረሰብ ወዳጅነትን መስበክም... ያው ዘረኝነት ነው። ለዚህም ነው፣ “የብሄረሰብ ወዳጅነትን እናስፋፋለን” ብለው፣ ብዙ ታሪክ እየጠቀሱ ከምር የሚጣጣሩ ሰዎች፣ ቅንጣት ታህል ሲሳካላቸው የማናየው። ምኞታቸው ቀና ቢሆንም፣ በአላዋቂነት፣ የዘረኝነት አስተሳሰብን ለማስፋፋት እያገዙ እንደሆኑ አይገነዘቡትም። የዘር ወዳጅነት የሚኖር ከሆነ፣ የዘር ጥላቻም ይኖራል። የጋራ ጉርሻ ካለ፣ የጋራ ረሃብም ይኖራል። መፈቃቀርን ለማስፋፋት፣ የዘረኝነት አስተሳሰብን መስበክ አያዋጣም። እናም፣ የዘረኝነት ወረርሽኝን ለመከላከል የምናቀርባቸው “ቀና ሰዎች”፣ ከዚህ ያለፈ አቅም ከሌላቸው፣ ከአመት አመት ዘረኝነት ሲባባስ ማየታችን እንዴት ይገርማል?
በበርካታ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ዘንድ የሚስተዋል ሌላ አዝማሚያም እንዲሁ ተስፋ ሰጪ አይደለም። ከፊሎቹ፣ እንደ ኢህአዴግ፣ በብሄረሰብ ቅኝት የተደራጁ ስለሆነ፣ ዘረኝነትን ከማስፋፋት በስተቀር፣ የዘረኝነት ወረርሽኝን ለማብረድና ለመግታት ይረዳሉ ብሎ ማሰብ፣ ከጭፍን ምኞት የተለየ ትርጉም አይኖረውም። እንደማንኛውም ሰው አስተሳሰባቸውን እያስተካከሉ እንዲሻሻሉ መመኘት ነው የሚሻለው።
“በብሔረሰብ ቅኝት መደራጀት ተገቢ አይደለም” የሚሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎችስ?
አንዳንዶቹ፣ የብሔረሰብ ወይም የጎሳ ዘረኝነትን፣ በ“አገራዊ ዘረኝነት” ለመተካት የሚሟሟቱ ናቸው። በትክክለኛው አሰያየም፣ “ብሔረተኛ” (nationalist) በሚል ልንጠራቸው እንችላለን። “የግል ማንነት” በማጣጣል፤ “አገራዊ ማንነት ይቅደም” ይላሉና። “ኢትዮጵያዊነት” እና “አንድነት” የሚሉ መፈክሮችን ከሚያዘወትሩ ከእነዚሁ ፓርቲዎች መካከል ብዙዎቹ፣ “አገር ትቅደም” የሚሉ ብሔረተኞች ቢሆኑም፣ በተደጋጋሚ እንዳየነው ግን፣ “ብሔር ብሔረሰብ ይቅደም” በሚሉ ፓርቲዎች ይዋጣሉ። ለምን? የግል ማንነትን ሲያጣጥሉና ሲያሳንሱ፣ አውቀውም ይሁን ሳያውቁ፣ “ዘረኝነትን” ስለሚያጠናከሩ ነው። “አገራዊ የጋራ ማንነት፣ አገራዊ የጋራ አእምሮና ህልውና” ካለ፤ “ብሄረሰባዊ የጋራ ማንነት፣ ጎሳዊ የጋራ አእምሮና ህልውና” ለምን አይኖርም? ለዚህ ጥያቄ፣ አሳማኝ ምላሽ ሊያቀርቡ አይችሉም። እናም፣ “አገራዊ ዘረኝነት”ን ለማስፋፋት በተጣጣሩ ቁጥር፣ በዚያው መጠን “ብሔረሰባዊ ወይም ጎሳዊ ዘረኝነትን” ለማስፋፋት አስተዋፅኦ ያደርጋሉ - አውቀውም ይሁን ሳያውቁ። ይሄ የአንዳንዶቹ ዝንባሌ ነው።
ሌሎቹ ደግሞ፣ “አገራዊ ማንነት ይቅደም” የሚል መፈክር ቢይዙም፤ ለጊዜው፣ ብዙውን ሕዝብ ለተቃውሞ ለማነሳሳት፣ “የብሄረሰብና የጎሳ ማንነት” የሚል የዘረኝነት ስሜትን ለመቀስቀሻነት ለመጠቀም ይሞክራሉ። በእርግጥ፣ የዘረኝነት ስሜትን የሚያራግቡት፣ “ለጊዜው ነው”፣ “ድል እስክናደርግ ድረስ ነው”፣ “ስልጣን ለመያዝ ያህል ብቻ ነው”... በማለት ራሳቸውን ያታልላሉ። ወይ ጉድ! ኢህአዴግም፣ “የብሄር ብሄረሰብ ፖለቲካ”፣ ጊዜያዊ መሳሪያ ነው እንደሚል አያውቁም? እንዴት ላያውቁ ይችላሉ? የህገመንግስት መግቢያ ላይ በፅሁፍ አስፍሮታል። ዘላቂው አላማዬ፣ “አንድ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ማህበረሰብ መፍጠር ነው” ይላል።
ለነገሩ፣ ኢህአዴጎች በፈርቀዳጅነት የሚያሞግሱት፣ “ዋለልኝ መኮንን”ም ከዚህ የተለየ ነገር አላለም። በ1960ዎቹ ዓ.ም፣ በዩኒቨርስቲ ኮሙኒስት ተማሪዎች ዘንድ፣ ጎልተው ከወጡት “ጀብደኛ መሪዎች” መካከል አንዱ የሆነው ዋለልኝ መኮንን፣ በብሔረሰብ ስም የተመሰረቱ ድርጅቶችንና ፓርቲዎችን መደገፍ አለብን በማለት ባቀረበው ፅሁፍ ነው እጅጉን የገነነው። መገንጠል የሚፈልጉ ድርጅቶችን ጭምር መደገፍ ብቻ ሳይሆን፣ በትጥቅና በስንቅ ማገዝ እንደሚያስፈልግ የገለፀው ዋለልኝ፣ የዚህ አስፈላጊነት ግን “ለጊዜው” ያህል ብቻ እንደሆነ ያስረዳል። ማለትም... ሕዝብን በስሜት ለማነቃነቅና መንግስትን ለማዳከም። ለጊዜው? ከጊዜ በኋላስ? ከዚያ በኋላማ፣ ግንባር ቀደሙ ኮሙኒስት ፓርቲ ስልጣን ሲይዝ፣ የብሄረሰብ ድርጅቶች እንደሚከስሙ ይገልፃል - ዋለልኝ። የዋለልኝ አድናቂዎች፣ ይህንን አስተሳሰብ፣ “ዲሞክራሲያዊ ብሄረተኝነት” ብለው ይጠሩታል። “ልማታዊ ብሄረተኝነት” ሲሉትም ያጋጥማል። ዋነኛው የዋለልኝ አድናዊ፣ ኢህአዴግ መሆኑን አትርሱ። በሌላ በኩልስ?
“ኢህአዴግ፣ ዘረኝነትን አስፋፍቷል” ብለው የሚያወግዙና፣ “ለጊዜው የዘረኝነት ቅስቀሳዎችን ብናካሂድ፣ ኢህአዴግን ለማዳከም ይጠቅመናል” ብለው የሚያስቡ ተቃዋሚ ፓርቲዎችስ? “ነፃ አውጪ፣ የአገራዊነት ጠበቃና የአንድነት ሃይል ነን” ሊሉ ይችላሉ። ግን፣ አስተሳሰባቸው፣ ከኢህአዴግና ከዋለልኝ በምንድነው የሚለየው?
“ዲሞክራሲያዊ ብሔረተኝነት”፣ “ልማታዊ ብሔረተኝነት”፣ “አገራዊ ብሔረተኝነት”፣ “ነፃ አውጪ ብሔረተኝነት”... በሚሉ ስያሜዎች መካከል፣ የቅፅል ልዩነት መኖሩ እውነት ቢሆንም፣... “ለጊዜው ብቻ ነው”፣ “ለመሸጋገሪያነት ያህል ነው” የሚሉ ማመካኛዎችን ቢለጠፉም፤ የሁሉም መዘዝ ተመሳሳይ ነው - የዘረኝነት ጥፋት። አንዳንዴ የኢትዮጵያ ነገር፣ ተስፋ አስቆራጭ ይመስላል የምለውም በዚህ በዚህ ምክንያት ጭምር ነው።                    

Page 7 of 19