የግብጽ የአቅርቦትና የንግድ ሚኒስትር ካሊድ ሃናፊ፤ የኢትዮጵያን የስጋ ምርት አሁን ከሚሸጥበት ባነሰ ቅናሽ ዋጋ ለመግዛትና ለዜጎች ለማቅረብ የሚቻልበትን ሁኔታ ለማመቻቸት  እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ባለፈው ረቡዕ ማስታወቃቸውን ዘ ካይሮ ፖስት ዘገበ፡፡ግብጽ የኢትዮጵያን የስጋ ምርት በቅናሽ ዋጋ በመግዛት በቶጎና በሌሎች የምዕራብ አገራት ለሚገኙ ግብጻውያን ማቅረብ የሚቻልበትን ሁኔታ ለመፍጠር በኢትዮጵያ የግብጽ አምባሳደር ከሆኑት አቡ በከር አል ሃናፊ እና በቶጎ የግብጽ አምባሳደር ከሆኑት ሞሃመድ ከሪም ሸሪፍ ጋር መወያየታቸውን ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡ግብጽ ከኢትዮጵያ ስጋ ለመግዛት ያሰበችበትን አዲሱን የቅናሽ ዋጋ በተመለከተ ሚኒስትሩ ያሉት ነገር ባይኖርም፣ በአገሪቱ ወቅታዊ ገበያ አንድ ኪሎ ስጋ ከ9.58 እስከ 11.1 ዶላር እየተሸጠ እንደሚገኝ ዘገባው ጠቁሟል፡፡ባለፈው መጋቢት ወር ላይ የግብጹ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ በሁለቱ አገራት ግንኙነት ዙሪያ መምከራቸውንና በወቅቱም የግብጽ ባለሃብቶች በአገራቱ መካከል ያለውን የኢኮኖሚና የንግድ ግንኙነት ለማሳደግ እየሰሩ እንደሚገኙ ለአገራቱ መሪዎች መግለጻቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ባለሃብቶቹ የኢንዱስትሪ ዞን እንዲቋቋም ወይም የትራንስፖርት ወጪን የሚቀንሱና የኢትዮጵያን ኢንዱስትሪ ለማሳደግ የሚያስችሉ ሌሎች እርምጃዎች እንዲወሰዱ መጠየቃቸውንም
አክሎ ገልጧል፡፡

Published in ዜና

    በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ  ከነሐሴ 1 ጀምሮ ለ15 ቀናት ሲፆም የቆየው የፍልሰታን ፆም መፈታት ተከትሎ በሥጋ ዋጋ ላይ ጭማሪ የሚያደርግ ማንኛውም ሥጋ ቤት ጥብቅ እርምጃ እንደሚወስድበት የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ አስታወቀ፡፡ የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ገመቺስ መላኩ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ በፆም ፍቺው ምክንያት በየቁም እንስሳት ነጋዴዎች ማህበር በኩል የሥጋ እጥረት እንዳይፈጠር ከበቂ በላይ በሬዎች የተገዙ ሲሆን በዓሉን ሰበብ በማድረግ ዋጋ የሚጨምሩ ካሉ ጥብቅ አስተዳደራዊ እርምጃ ይወሰድባቸዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በማህበራቸው በኩል ተጠያቂ ይሆናሉ ብለዋል - ኃላፊው፡፡ ከሥጋ አቅርቦት ጋር በተያያዘ ምንም አይነት ክፍተት እንደማይፈጠር ያረጋገጡት አቶ ገመቺስ፤ ህብረተሰቡ የዋጋ ጭማሪ ካጋጠመው
በ8588 ደውሎ ጥቆማ በማድረስ፣ በንግድ ስርአት ውስጥ የሚታየውን ህገ-ወጥነት ሊታገል እንደሚገባው አበክረው አሳስበዋል፡፡

Published in ዜና

     በዘንድሮው ክረምት ሦስት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በአዲስ አበባ ከተማ 14 ሰዎች በውሃ አደጋ ህይወታቸውን ያጡ ሲሆን ባለፈው ዓመት ክረምት ከደረሰው አደጋ በእጥፍ ጨምሯል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ እሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መቆጣጠር ባለስልጣን የኮሙኒኬሽን ባለሙያ አቶ ኪዳነ አብርሃ ለአዲስ አድማስ
እንደገለፁት፤ ክረምቱ ከገባበት ሰኔ 1 ጀምሮ እስከ ትናንት በስቲያ 15 የውሃ አደጋዎች ደርሰው የ14 ሰዎችን ህይወት ቀጥፈዋል፡፡ አብዛኞቹ በኩሬና በወንዞች ውስጥ ለመዋኘት ሲሞክሩ ሰጥመው መሞታቸውን አቶ ኪዳነ ገልፀዋል፡፡ አደጋዎቹ በብዛት ያጋጠሙት በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ሃና ማሪያም አካባቢ በሚገኙ ሁለት ኩሬዎች ውስጥ ሲሆን በእነዚህ ኩሬዎች 6 ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል ተብሏል፡፡ በጀሞ የኮንዶሚኒየም ሳይት ለቤቶች ግንባታ ለሚውል ጠጠር ማምረቻ በተቆፈረ ጉድጓድ ውስጥ በተጠራቀመ የኩሬ ውሃ ደግሞ 3 ሴት ህፃናት ገብተው መሞታቸውን የባለስልጣኑ መረጃ ያመለክታል፡፡ ባለፈው ዓመት የክረምት ወቅት 21 የውሃ አደጋዎች አጋጥመው የ8 ሰዎች ህይወት ሲጠፋ፣ ዘንድሮ 15 አደጋዎች አጋጥመው የ14 ሰዎችን ህይወት ቀጥፏል፡፡  ዓምና ክረምት ላይ መንገድ ዳር በተቆፈረ ጉድጓድ ውስጥ ገብቶ የሞተ ሰው እንደሌለ የጠቆመው የባለስልጣኑ ሪፖርት፤ ዘንድሮ በዓለም ባንክና በቱሉ ዲምቱ አካባቢ የ60 እና የ65 ዓመት አዛውንቶችን ጨምሮ 3 ሰዎች ጉድጓድ ውስጥ ሞተው መገኘታቸውን ገልጿል፡፡ ክረምት ት/ቤት የሚዘጋበት ወቅት በመሆኑ ህፃናትና ታዳጊዎች ዋና ለመለማመድ በሚል ወንዝና ኩሬ ውስጥ እየሰመጡ የሚሞቱ ሲሆን ወንዝ ይዞ የሚመጣን ቁሳቁስ ለመለቃቀም ሲሞክሩም በውሃ የመወሰድ አደጋዎች እንደሚያጋጥሙ አቶ ኪዳነ ተናግረዋል፡፡ ህብረተሰቡ በተለይ ወላጆች፣ ልጆቻቸው ወደነዚህ ቦታዎች እንዳይጠጉ በማድረግ አደጋውን መከላከል ያሻል ያሉት አቶ ኪዳነ፤ ጎርፍ አቅጣጫውን ስቶ ወደ መኖሪያ ቤቶች እንዳይገባም ቱቦዎችን  ከደረቅ ቆሻሻ መጠበቅ አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡ ማናቸውም የመንግስት አካላትም ሆኑ ሌሎች ወገኖች ለተለያዩ ዓላማዎች የቆፈሩትን ጉድጓድ መልሰው እንዲደፍኑ ያሳሰቡት
የባለስልጣኑ የኮሙኒኬሽን ባለሙያ፤ ሁሉም ሃላፊነቱን በመወጣት አደጋውን መቀነስ እንዳለበት ተናግረዋል፡፡  





Published in ዜና

     በመጪው ጥቅምት የ70ኛ አመት የምስረታ በዓሉን የሚያከብረው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ ኢትዮጵያና የቀድሞው የአገሪቱ መሪ ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ በድርጅቱ መስራች አባልነት ያበረከቱትን አስተዋጽኦ የሚዘክርና የበዓሉ አካል የሆነ ልዩ ፕሮግራም ማካሄዱን ታዲያስ መጽሄት ዘገበ፡፡
ኒውዮርክ ሲቲ ውስጥ በሚገኘው የተመድ ዋና ጽህፈት ቤት ከትናንት በስቲያ በተከናወነው በዚህ ልዩ ፕሮግራም ላይ አለማቀፍ እውቅና ያላቸው የታሪክ ተመራማሪዎች፣ ጸሃፊያንና በተመድ የቀድሞው የኢትዮጵያ ልኡክ ዶክተር ግርማ አበበ፤ ቀዳማዊ ሃይለ ስላሴ በተመድ የነበራቸውን ሚና በተመለከተ ንግግር አድርገዋል፡፡ቀዳማዊ ሃይለ ስላሴ በሊግ ኦፍ ኔሽንስ ያበረከቱትን አስተዋጽኦ የሚያሳይ ዘጋቢ ፊልምና ንጉሱ እ.ኤ.አ በ1963 በተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ በዋይት ሃውስና በሌሎች መድረኮች ላይ ያደረጓቸውን ንግግሮች የሚያሳዩ የቪዲዮ ምስሎች ለታዳሚው ቀርበዋል፡፡በተመድ የቀድሞው የኢትዮጵያ ልኡክና የተመድ ጽህፈት ቤት የፖለቲካ ጉዳዮች ክፍል ምክትል ዳይሬክተር የነበሩት ዶ/ር ግርማ አበበ ባደረጉት ንግግር፤ ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ስብሰባዎች ላይ ያደረጓቸውን በሰላም፣ በጸጥታና በሰብዓዊ
መብቶች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ ንግግሮችን ዳስሰዋል፡፡

Published in ዜና

“በካህናትና ሠራተኞች ስም የሚደረግ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ተቀባይነት የለውም”

    በቤተ ክርስቲያኒቱ ሀብት፣ ዘረፋ እና ምዝበራ ጥፋታቸው የተረጋገጠባቸው የአድባራት እና የሀገረ ስብከት ሙሰኛ ሓላፊዎች ለሕግ ተጠያቂነት ተላልፈው እንደሚሰጡ፣ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ተናገሩ፡፡የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች እንደጠቆሙት፣ ፓትርያርኩ ይህን የማረጋገጫ ቃል የተናገሩት፣ ስለ አድባራቱ የመሬት፣ የሕንጻ እና የልዩ ልዩ ገቢ ማስገኛ ተቋማት ኪራይ ተመን በተካሔደው ጥናታዊ ሪፖርት ላይ የሀገረ ስብከቱን ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ማእምራን የማነ ዘመንፈስ ቅዱስ፤ ባለፈው ማክሰኞ ጠዋት በጽ/ቤታቸው ባነጋገሩበት ወቅት ነው፡፡ጥናታዊ ሪፖርቱ፣ ‹‹አድሏዊ እና ግለሰቦችን ለማጥቃት የተደረገ ነው›› በሚል በአንዳንድ አድባራት ተቃውሞ ማስነሣቱን ዋና ሥራ አስኪያጁ ለፓትርያርኩ ጠቅሰዋል፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ አስተዳደር ጉባኤ፣ የጥናታዊ ሪፖርቱን የመፍትሔ ሐሳቦች በሙሉ ድምፅ በመቀበል፣ የአድባራቱ ሓላፊዎች ጥፋት በሕግ አግባብ እንዲታይና ክሥ እንዲመሠረትባቸው ያሳለፈው ውሳኔም ሌላ አማራጭ
እንዲፈለግለት ፓትርያርኩን ጠይቀዋል ተብሏል፡፡ ጥናቱ፣ ራሳቸው በሰጡት ትእዛዝ እና የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ አስተዳደር ጉባኤ ባቋቋመው ኮሚቴ በይፋ መካሄዱን ያስታወሱት ፓትርያርኩ፣ ሪፖርቱን ለመቃወም በሚል ካህናትንና ልዩ ልዩ ሠራተኞችን በማደራጀት በጎን የሚቀርብላቸውን አቤቱታ እንደማይቀበሉት ለዋና ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል፡፡‹‹ለማንም ሰው ከለላ መኾን አልፈልግም፤ ሽፋንም አልሰጥም፤ ለአንተም ጨምሮ፤›› በማለት አቋማቸውን ያረጋገጡት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ ‹‹በዚኽ አጸያፊ የዘረፋና የምዝበራ ሥራ ውስጥ እጁ የተገኘበትን ሰው ኹሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ አሳልፋ ትሰጣለች፤ ይኼ የመጨረሻ አቋሜ ነው፤›› ሲሉ የሕግ ተጠያቂነቱ አይቀሬ መኾኑን አስታውቀዋል፡፡በፓትርያርኩ ጠንካራ አቋም መደናገጥ ታይቶባቸዋል የተባሉት ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ በሀገረ ስብከቱ ተከማችተው ለቆዩትና በየአድባራቱ እየተባባሱ ለመጡት የሙስና እና የመልካም አስተዳደር ዕጦት ችግሮች የአሠራር ማሻሻያዎችን በመተግበር ላይ እንደሚገኝ በማስረዳት፣ ጥናታዊ ሪፖርቱን እንደሚቀበሉትና እንደሚደግፉት ለፓትርያርኩ እንደገለፀላቸው ታውቋል፡፡
ላለፉት ስድስት ወራት በ58 አድባራት ላይ ሲካሔድ የቆየው ጥናት፣ ከሓላፊዎቹ ጋር የጥቅም ትስስር ለፈጠሩ ግለሰቦች በሚያደሉ ውሎች የቤተ ክርስቲያኒቱ መሬት፣ ሕንጻዎች፣ ሱቆች እና ልዩ ልዩ የገቢ ማስገኛ ተቋማት ላይ የተጧጧፈ ዘረፋና ምዝበራ መፈፀሙን አረጋግጧል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ ሀብትና ንብረቷን ከብክነት ለመታደግ ያወጣችውን የቃለ ዐዋዲ ደንብ ማስከበር የሚገባው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትም፤ ከድንጋጌው ውጭ ለተሠሩ ሥራዎች ዕውቅና በመስጠት የሕግ ጥሰቱ አካል እንጂ የሕግ አስፈጻሚ መኾን
አለመቻሉ የችግሩ ባለቤት እንደሚያደርገው በሪፖርቱ ተጠቁሟል፡፡

Published in ዜና

ከ400 በላይ የአገር ውስጥና የውጭ ሀገራት ተሣታፊዎች የሚካፈሉበትና ከ500ሺ በላይ ሰዎች ይጐበኙታል ተብሎ የሚጠበቀው “አበሻ አዲስ አመት ኤክስፖ 2008” ዛሬ ይከፈታል፡፡
የቀድሞው ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደጊዮርጊስና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ቴዎድሮስ አድሃኖምን ጨምሮ ሌሎች ታላላቅ የመንግስት ባለስልጣናት በእንግድነት ይገኙበታል በተባለው በዚህ የአዲስ አመት ኤክስፖ ላይ ከ100 በላይ የአገሪቱ ታላላቅ ድምፃውያንና ኮሜዲያን ሥራዎቻቸውን ለጐብኚዎች ያቀርባሉ ተብሏል፡፡
ለሃያ አንድ ቀናት በሚቆየው በዚህ ኤክስፖ፤ የአለማችንን ትልቁ የሻማ ዛፍ የማብራት ሥነስርዓት እንደሚካሄድም ታውቋል፡፡

Published in ዜና

  የበር እጀታ የጉንፋን ቫይረስን ሊያስተላልፍ ይችላል
                        
       ጉንፋንን ከቅዝቀዜና ብርድ ጋር በቀጥታ የሚያገናኘው ነገር ባይኖርም እንዲህ እንደ አሁኑ ክረምት በሚሆንበት ወቅት ብዙዎቻችን ለጉንፋን መጋለጣችን አይቀሬ ነው፡፡ ዝናብ፣ ብርድና መጥፎ ሽታ ለጉንፋን መከሰት የራሳቸውን ድርሻ የሚያበረክቱ ቢሆንም ዋናው የጉንፋን መንስኤ ግን ቫይረስ ነው፡፡ ጉንፋን ለማስያዝ የሚችሉ ከ200 በላይ የቫይረስ ዝርያዎች አሉ፡፡ ከእነዚህ ሁሉ ቫይረሶች መካከል በመተላለፍ አቅማቸውና በስፋት በመታየታቸው ቀዳሚነቱን የሚይዙት ራይኖ ቫይረስ የተባሉት ጉንፋን አምጪ ቫይረሶች ናቸው፡፡ ለመሆኑ ለጉንፋን አጋላጭ ሁኔታዎች ምንድናቸው? ህክምናስ አለው? መከላከያዎቹስ? እነዚህንና መሰል ጉዳዮችን በተመለከተ Journal of Medicine በቅርቡ ለንባብ ያበቃውን መረጃ እንደሚከተለው አቅርበንላችኋል፡፡
የጉንፋን መንስኤ
ጉንፋንን ሊያስይዙ የሚችሉ የቫይረስ ዝርያዎች 200 ይደርሳሉ፡፡ በስፋት የሚታወቀውና ከሰው ወደ ሰው በቀላሉ የመተላለፍ አቅም ያለው ቫይረስ፣ጉንፋን አምጪ ቫይረስ ነው፡፡ ጉንፋን የላይኛው የመተንፈሻ ስርዓታችን አካል የሆኑትን አፍንጫና ጉሮሮ የሚያጠቃ ህመም ነው፡፡ ጉንፋን ራሱ የሚተውና ቶሎ የሚድን ህመም ቢሆንም የአፍንጫና የጉሮሮ ቁስለቱ፣ ራስ ምታቱና የመገጣጠሚያ ህመሞችን ማስከተሉ፣ ታማሚውን ምቾት የሚነሳ ሲሆን አንዳንዴ ለጥቂት ቀናትም ቢሆን አልጋ ሊያስይዝ የሚችል ህመም ነው፡፡
ጉንፋን የዕድሜና የፆታ ልዩነት ሳያደርግ ሁሉንም ሰው ሊይዝ የሚችል ህመም ቢሆንም ከአዋቂዎች ይልቅ ልጆች በጉንፋን ቶሎ ቶሎ የመያዝ ዕድሉ አላቸው፡፡ አዋቂዎች በአብዛኛው በዓመት አራት ጊዜ ያህል በጉንፋን ሲያዙ፣ ልጆች በዓመት ደግሞ 10 ጊዜ ያህል  በጉንፋን የመያዝ አጋጣሚ ይኖራቸዋል፡፡
የጉንፋን ቫይረስ ወደ ሰውነታችን ውስጥ የሚገባው በአፍና በአፍንጫችን በኩል ሲሆን ከዚህ በተጨማሪ በመጨባበጥና እንደ ስልክ፣ ፎጣ፣ የበር እጀታ ያሉ በጋራ ጥቅም ላይ በሚውሉ ቁሳቁሶችም አማካይነት ሊተላለፍ ይችላል፡፡ ጉንፋንን በማስተላለፍ ረገድ ከትንፋሽ የበለጠ መጨባበጥ ከፍተኛውን ስፍራ እንደሚይዝም Journal of Medicine ይጠቁማል፡፡ በጉንፋን የተያዘ ሰው ከአፍንጫው የሚወጣውን ፈሳሽ ያስወገደበት እጁ ላይ ጉንፋን አምጪው ቫይረስ ረዘም ላለ ጊዜ የሚቆይ በመሆኑ፣ ይህንን በጉንፋኑ ቫይረስ የተበከለ እጅ የጨበጠ ሰው በቀላሉ በበሽታው የመያዝ ዕድል ይኖረዋልና ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል፡፡
ጉንፋን የሚያስከትለው የጤና ችግር
ጉንፋን አብዛኛውን ጊዜ እንደ ቀላል የሚታይና በቀናትና በሳምንታት ጊዜ ውስጥ ሊድን የሚችል በሽታ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ አንዳንድ ጊዜ ጉንፋን ህመምተኛውን አልጋ ከማስያዝም በላይ ሌሎች ጠንቆችንም ሊያስከትል የሚችል የጤና ችግር ነው፡፡ ይህ ጉዳይ በተለይም በህፃናትና በልጆች ላይ ጎልቶ የሚታይ ሲሆን በጉንፋን የተያዙ ልጆች የጆሮ ኢንፌክሽን ችግሮች ሲያጋጥሟቸው ይታያል፡፡ ይህም በከባድ ራስ ምታት፣ በጆሮ ህመም ስሜት፣ በትኩሳትና አረንጓዴ ፈሳሽ በአፍንጫ በኩል በማውጣት ይገለፃል፡፡ ጉንፋን በተለያዩ መንገዶች የቤት ውስጥ ህክምና በማድረግና እረፍት በመውሰድ ሊድን የሚችል ህመም ሲሆን ቶሎ የማይድን ጉንፋን ለሳይነስ፣ ለጉሮሮ ኢንፌክሽን፣ ለኒሞኒያና ብሮንካይትስ የማጋለጥ ዕድል አለው፡፡
ጉንፋን ለምን ደጋግሞ ይከሰታል?
የሰው ልጅ በሽታን የመከላከል አቅም ከሚለካባቸው ቀላል ህመሞች አንዱ ጉንፋን ነው፡፡ በየጊዜው በጉንፋን እየተያዙ የሚተኙ ሰዎች በሽታን የመከላከል አቅማቸው የተዳከመ መሆኑን የሚያሳይ ምልክት ነው፡፡ በእርግጥ በጉንፋን በተደጋጋሚ ለመያዝ ዕድሜ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያደርጋል። ከአዋቂዎች ይልቅ ልጆች በጉንፋን የመያዝ ዕድላቸው ከፍ ያለ ነው፡፡ ሰዎች በተፈጥሮአቸው ዕድሜያቸው እየጨመረ ሲሄድ፣ ለአብዛኛዎቹ የጉንፋን ቫይረሶች መቋቋሚያ የሚሆን አቅምን እያደረጁ ይሄዳሉ። ስለዚህም በጉንፋን የመያዝ ዕድላቸው ይቀንሳል። እንደ ስኳር፣አስምና ኤችአይቪ ያሉ ህመሞች ያሉባቸው ሰዎች፣ በጉንፋን ቶሎ ቶሎ የመያዝ ዕድላቸው ከፍተኛ ሲሆን በቶሎ ለመዳንም ይቸገራሉ፡፡
ጉንፋን መድኀኒት አለው?
ጉንፋንን ሊያድን የሚችል መድኀኒት አለመኖሩን Journal of Medicine ጠቁሟል፡፡ ብዙ ጊዜ ሰዎች በጉንፋን በሚያዙበት ወቅት ፀረ ባክቴሪያ መድኀኒቶችን ይጠቀማሉ፡፡ ይህ ግን ውሉን የሳተ ነው፡፡ ለምን ቢሉ? የጉንፋን መነሻው ቫይረስ እንጂ ባክቴሪያ አይደለም፡፡ ስለዚህም እንደ አሞክሳሲሊን ባሉ ፀረ - ባክቴሪያ መድኀኒቶች ጉንፋንን ለማከም መሞከሩ ብልህነት የጎደለው መሆኑን ጆርናሉ ያመለክታል፡፡ በጉንፋን ህመም ወቅት የሚወሰዱ የተለያዩ የህመም ማስታገሻ መድኀኒቶች ከጉንፋን ጋር በተደራቢነት ያሉትን እንደ ራስ ምታት፣ ትኩሳት የመሳሰሉት  የሚያስከትሉትን የህመም ስሜት ለማስታገስ ከመርዳታቸው ውጭ ለጉንፋን ህመሙ የሚሰጡት አንዳችም ፋይዳ የለም፡፡ ከዚህ ይልቅ በቤት ውስጥ የሚደረጉ ህክምናዎች በሽታውን በቶሎ ለማዳን ያስችላሉ፡፡
ሰዎች በጉንፋን በሽታ በሚያዙበት ወቅት በቂ እረፍት ማድረግ እንደሚገባቸው የሚጠቁመው ጆርናሉ፤ ይህም ለታማሚዎቹ ብቻ ሳይሆን ከታማሚዎቹ ጋር አብረው የሚሰሩና በተለያዩ ምክንያቶች የሚገናኙ ሰዎች በበሽታው እንዳይያዙ ለማድረግ እንደሚረዳም ገልጿል፡፡
ጉንፋንን የማከሚያ መንገዶች
በጉንፋን ሲያዙ በቂ እረፍት በሚያደርጉበት ቤትዎ ውስጥ ሆነው በሽታዎን በተለያዩ መንገዶች ማከም ይችላሉ፡፡ ከእነዚህ የጉንፋን በሽታ ማከሚያ መንገዶች መካከል፡- ብዙ ፈሳሾችን መውሰድ፣ ውሃ፣ የፍራፍሬ ጭማቂዎች፣ ሾርባ፣ ሻይና አጥሚት መሰል ትኩስ መጠጦችን ቶሎ ቶሎ መጠጣት የሚያስፈልግ ሲሆን ይህም በላብና በአፍንጫችን የሚወጡ ፈሳሾችን ለመተካትና የሰውነትን የውሃ ሚዛን ለመጠበቅ ይረዳል። ካፌይንና አልኮልነት ያላቸው መጠጦች በሰውነታችን ውስጥ የሚገኘውን ውሃ የመምጠጥ ባህርይ ስለአላቸው በጉንፋን በተያዙ ወቅት እነዚህን መጠጦች ከመጠቀም ይቆጠቡ። ትኩስ መጠጦችን በተለይ ሾርባዎችን (የዶሮ ሾርባ) መጠጣት የጉንፋንዎን ዕድሜ ለማሳጠር ይጠቅማል። አንዳችም ሳይንሳዊ ህክምና፣ መድኀኒትና ክትባት ያልተገኘለት የጉንፋን በሽታ፤ በቀላሉና የግል ንፅህናን በአግባቡ በመጠበቅ ብቻ ልንከላከለው የምንችለው በሽታ ስለሆነ ሁልጊዜም ለንፅህናዎ ትኩረት ይስጡ። በሚስሉና በሚያስነጥሱ ጊዜ መሃረብ ወይም ሶፍትን መጠቀም አይዘንጉ፡፡ እጅዎን ከመታጠብዎ በፊት ፊትዎንና አፍንጫዎን ከመነካካትም ሆነ ወደ ገበታ ከመቅረብ ይቆጠቡ፡፡  

        ጉንፋንዎን በቤትዎ ያክሙ

   ነጭ ሽንኩርት
ከፀረ ባክቴሪያና ፀረ ፈንገስ ባህሪው በተጨማሪ በጉሮሮ አካባቢ የሚከሰቱ ቁስሎችን ለማከም ይረዳል፡፡ ነጭ ሽንኩርት አስም፣ የአፍንጫና የጉሮሮ ህመሞችን ያስታግሳል፡፡ ነጭ ሽንኩርትን መቀቀል መድኀኒትነት ያለውን ኦሊሲን የተባለ ንጥረ ነገር ስለሚያጠፋው በጥሬው ከትፈው ቢወስዱት የጉሮሮ ህመምና ጉንፋንዎን ድራሹን ሊያጠፋልዎት ይችላሉ፡፡

      ቀረፋ
ቀረፋ ጉንፋንና ኢንፍሉዌንዛን በመፈወስ ረገድ ከፍተኛ ሚናን ይጫወታል፡፡ ጥቂት የቀረፋ ዱቄትን በሞቀ ውሃ ውስጥ ጨምረው ይጠጡት፡፡ ከጉንፋንዎና ኢንፍሌዌንዛዎ እፎይታን ያገኛሉ፡፡ ይሁን እንጂ በርካታ መጠን ያለውን ቀረፋ መጠቀም ችግር ሊያስከትልብዎ ይችላልና ይጠንቀቁ፡፡ በተለይም ነፍሰጡር ሴቶችና የሚያጠቡ እናቶች ቀረፉን በፍፁም መጠቀም የለባቸውም፡፡



     ዝንጅብል
ደረት ላይ ለሚሰማ ጉንፋንና ኢንፍሉዌንዛ በግማሽ ሊትር ውሃ ውስጥ 3 ማንኪያ የዝንጅብል ዱቄት መታጠቢያ ገንዳ ውስጥ ጨምረው ይታጠቡ፡፡ በጉንፋንዎ ሳቢያ የምግብ መዋጥ ችግር ካጋጠምዎ ዝንጅብል አፍልተው ይጠጡበት፡፡ የማቅለሽለሽ ስሜትን በማጥፋት የአፍና የጉሮሮዎ አካባቢ ምግብ እንዲቀበል ያደርግልዎታል፡፡


      የዶሮ ሾርባ
የዶሮ ሾርባ ለጉንፋንና ለኢንፍሉዌንዛ በሽታዎች ፍቱን መድኀኒት ሆኖ ለዓመታት ዘልቋል፡፡ በአትክልቶችና ቅመሞች ተከሽኖ የተሰራ የዶሮ ሾርባ በጉንፋን ሳቢያ የሚከሰተውን የአፍንጫ መዘጋት ይከፍታል፡፡

          ማር
ማር፣ ሎሚና ሙቅ ውሃ ከፍተኛ ህመም ያለውን የጉንፋን በሽታና ሳልን ለማስታገስ ይረዳል፡፡ ማርን በትኩስ ወተት መጠጣት ህመሙ እንዲታገስና እንቅልፍ እንዲወስድዎ ያግዛል፡፡

        ሎሚ  
ሎሚ ለተለያዩ የጤና ችግሮች ፍቱን መድኀኒት ነው፡፡ ጉንፋንዎ በአፍንጫዎ ላይ ጉዳት ካስከተለና አፍንጫዎ ችግሩን ቀጭን ፈሳሽ በማውጣት እየገለፀልዎ ከሆነ በአንድ ብርጭቆ የፈላ ውሃ ውስጥ ሁለት ሎሚዎችን ጨምቀው በትኩሱ ይጠጡበት፡፡ ጉንፋንዎ መሻሻልን እንዳሳየ አፍንጫዎ ፈሳሹን በማቆሙ ሊረዱት ይችላሉ፡፡ ሎሚ ለአስም፣ ለጉንፋንና ለብሮንካይትስ ህመሞች ማስታገሻነት ያገለግላል፡፡

Published in ዋናው ጤና

ለኩላሊት ንቅለ ተከላ ሕክምና ወሳኝ የሆነ አዲስ የላብራቶሪ ምርመራ በኢትዮጵያ የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲቲዩት (ፓስተር) የተጀመረ ሲሆን ምርመራው የኩላሊት ንቅለ ተከላ ህክምና በቅርቡ እንዲጀመር የሚያስችል ነው ተብሏል፡፡ ኢንስቲቲዩቱ ቀደም ሲል በአገሪቱ ያልነበሩና በውጭ አገር እጅግ ከፍተኛ ዋጋ የሚያስወጡ  የላብራቶሪ ምርመራዎችን ለማድረግ በሚያስችል መሣሪያና የሰው ኃይል እንደተደራጀ ታውቋል፡፡
ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በተደረገለት የ13 ሚሊዮን ብር የገንዘብ ድጋፍ በተደራጀው የላብራቶሪ ምርመራ አገልግሎት፤ የጥቁር አንበሳ፣ የቅዱስ ጳውሎስ፣ አለርት፣ ቅዱስ ጴጥሮስና የአማኑኤል የአዕምሮ ህክምና ስፔሻላይዝድ ሆስፒታሎች ተጠቃሚ እንደሚሆኑ የተገለጸ ሲሆን በተለያዩ ምክንያቶች በሆስፒታሎቹ ለሚቋረጡ የላብራቶሪ ምርመራዎችም አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ላለፉት ስድስት ወራት በጥቁር አንበሳ፣ በጳውሎስና በአማኑኤል ሆስፒታሎች የሙከራ አገልግሎት ሲሰጥ መቆየቱን የገለፁት የኢንስቲቲዩቱ ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር አምሃ ከበደ፤ በቅርቡ በአምስቱ ሪፈራል ሆስፒታሎች አገልግሎቱን ለመስጠት የሚያስችል ዝግጅት መደረጉን ተናግረዋል፡፡ ከአምስቱ ሆስፒታሎች ተወካዮች ጋር የስምምነት ሰነድም ተፈራርመዋል፡፡
ኢንስቲቲዩቱ እስከዛሬ በአገሪቱ ያልነበሩ፣አዳዲስ የላብራቶሪ ምርመራ አገልግሎቶችን ለመስጠት በሚያስችል ዘመናዊ መሳሪያዎችና ባለሙያዎች መደራጀቱን የገለፁት የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ ዶ/ር ከሰተብርሃን አድማሱ፤ ወደፊት ሁሉም አይነት የላብራቶሪ ምርመራዎችን በአገር ውስጥ ለማድረግ ጥቂት ሥራዎች ብቻ እንደሚቀሩና እነዚህን በማሟላት ሙሉ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር ተናግረዋል፡፡
የቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ ሜዲካል ዲያሬክተር ዶ/ር ዘሪሁን አበበ በሰጡት አስተያየት፤#የኩላሊት ንቅለ ተከላ ህክምናን በአገሪቱ ለመጀመር የሚደረገውን ጥረት የላብራቶሪ ምርመራ አገልግሎቱ በእጅጉ ያግዘዋል; ብለዋል፡፡

Published in ዋናው ጤና
Saturday, 15 August 2015 16:20

የየአገሩ ምሳሌያዊ አባባል

ከተጠበሰ እንቁላል ጫጩት ማስፈልፈል አትችልም፡፡
የደች አባባል
 መደነቅ የጥበብ መጀመሪያ ነው፡፡
የግሪካውያን አባባል
እግዚአብሔር ምድር ላይ ቢኖር ኖሮ ሰዎች መስኮቱን ይሰብሩት ነበር፡፡
የአይሁዳውያን አባባል
ዝምታ ፈፅሞ ተፅፎ አያውቅም፡፡
የጣልያውያን አባባል
ፖለሪካ የበሰበሰ እንቁላል ነው፤ ከተሰበረ ይገማል።
የሩሳያውያን አባባል
ከተራመድክ መደነስ ትችላለህ፤ ከተናገርክ መዝፈን ትችላለህ፡፡
የዚምባቡዌ አባባል
እንደ ንፁህ ህሎሊና ለስላሳ ትራስ የለም፡፡
የፈረንሳውያን አባባል
ዝም ብለህ ተቀመጥ፤ ሰዎች እንደፈላስፋ ይቆጥሩሃል፡፡
የላቲን አባባል
የእግዚአብሔር እርሳስ ላጲስ የለውም፡፡
የሃይቲዎች አባባል
የማትናከስ ከሆነ ጥርስህን አታሳይ፡፡
የስፔናውያን አባባል
የጤናማነት መጀመሪያ በሽታውን ማወቅ ነው፡፡
የስፔናውያን አባባል
የስኳርን ጣዕም የምታደንቀው ሎሚን ስትቀምስ ብቻ ነው፡፡
የዩክሬናውያን አባባል
የቱንም ያህል ብትደክም ኮርማ ወተት አይሰጥህም፡፡
የዩክሬናውያን አባባል
ብቻውን የተጓዘ ያሻውን ማውራት ይችላል፡፡
የሩዋንዳውያን አባባል
ሚስትህን በአበባም እንኳ አትምታት፡፡
የሂንዱ አባባል
ማንም የራሱን አይብ ኮምጣጣ ነው አይልም፡፡
የአፍጋኒስታውያን አባባል
ሁሉም ሰው እንዲራመድብህ ከፈቀድክ ምንጣፍ ትሆናለህ፡፡
የቡልጋሪያውያን አባባል
የውሃውን ጥልቀት በሁለት እግሮቹ የሚለካ ጅል ብቻ ነው፡፡
የአፍሪካውያን አባባል
መንገዶች ሁሉ ወደሮም አያደርሱም፡፡
የስሎቬንያውያን አባባል
ድልድዩን ከሰበርክ ዋና መቻልህን እርግጠኛ ሁን፡፡
የስዋሂሊ አባባል

Published in ጥበብ
Saturday, 15 August 2015 16:19

ቡሄ

  ቡሄ ጨፋሪ ልጆችን ለመምረጥ የተለያየ ሃሳብ አቅርበን ነበር፡፡ “እገሌ ይረብሻል----ድምፁ ያስጠላል----ሣንቲም ያጨናብራል!” ወዘተ እያልን ብዙ ተናቆርን፡፡ የማታ ማታ ግን ከመሃላችን እንደ ትልቅ ሰው የምናየው ባህሩ፣ አስታረቀንና ስምንት ልጆች ቡድን ሠራን፡፡
ስምንት መሆናችን የምንካፈላትን ሣንቲም ያሳሳል ብለው የሰጉ ነበሩ፡፡ እነሱ ስድስት እንድንሆን መከሩ። ግን ከምርጫው ሊወገዱ የታሰቡት ዳኜና ሻውል ዓይናቸውን ሲያቁለጨልጩ አሳዘኑን፡፡
“በቃ - ይሁኑ - ይሁኑ!” አልን፡፡
በቀለ ግን እንድናስገባው ቢጐተጉተንም በአንድ ድምፅ እምቢ አልነው፡፡ ብናስገባው ገንዘብ ያዥ ካልሆንኩ ይላል፡፡ ገንዘብ ያዥ ሲደረግ ደግሞ፣ ብር ሠርቆ ወይ ካልሲ ውስጥ አሊያም የውስጥ ሱሪው ውስጥ ይወሽቃል። ያኔ ጭቅጭቅ ይፈጠርና ጭፈራችን ይበላሻል፡፡ ከዚህ በፊት ሁለቴ እንዲህ አድርጎናል፡፡
ልጆች ከተመራረጥን በኋላ ደህና ገንዘብና ጥሩ ሙልሙል የሚሰጡንን ሰዎች ቤት ለየን፡፡ ማን ጥሩ እንደሚሰጥ፣ ማን እንደሚሰስት ከልምድ እናውቀዋለን፡፡ የስፖርት ሣንቲም ስንጠይቅና በሆያ ሆዬ ብዙ ተምረናል።  
የመጀመሪያ ምርጫችን ጋሽ ሰብስቤ ነበር፡፡ ጋሽ ሰብስቤ መቼም ቢሆን ልጆች ከጠየቁት ብሩን መዥርጦ የሚሰጥ ቸር የጓደኛችን አባት ነው። በክላሰር ላይ የአሥራ አንድ ተጫዋቾችን ሥዕል ደረታችን ላይ እንደ አኮርድዮን ዘርግተን ስንሄድ፣ አምስት ብር ስለሚሰጠን እሱ ሲገጥመን እንደ ሎተሪ ነው የምንቆጥረው፡፡ ሌላው የቡሄ ጭፈራ ምርጫችን የእትዬ የውብዳር ግሮሠሪ ነው፡፡ እትዬ የውብዳር ግሮሠሪ፣ በተለይ በበዓል ሰሞን አዝማሪ ስለሚኖርና የከተማው ትልልቅ ሰዎች ስለሚሰበሰቡ አንዱ አንዱን እያየ ብሩን እንደሚመዝ አሳምረን እናውቃለን፡፡ ሥጋታችን ምናልባት ዛሬም በቀለ እየተከታተለ እንዳይረብሸን ነው፡፡ በቀለ ተንኮለኛ ስለሆነ ሸር እንዳይሠራብን በሚል እኔ ገንዘብ ያዥ ሆንኩ፡፡ ግጥም አውጪ ፈለቀ ሆነ፡፡ እኔ ጠንቃቃ በመሆኔ፣ ፈለቀ ደግሞ ምርጥ ድምጽ ስላለው ተመረጥን፡፡
እኔ ግን ልቤ አልተረጋጋም፡፡ በቀለን አውቀዋለሁ። ተንኮል ሲሸርብ የሚችለው የለም፡፡ ከእጅ ላይ እንኳ ሲቀማ እንደ ጭልፊት ነው፡፡ ሩጫማ… ሰጐን ነው። የልቡን ለማድረስ ልስላሴው አያድርስ ነው፡፡ እንደ ዔሊ አንገቱን ቀብሮ ሲረግጡት እንኳ ድንጋይ ይሆናል፡፡ ችግሩ የሚገለጠው ከተፈፀመ በኋላ ነው። የሆኖ ሆኖ ብቻ ቡድናችን ተናካሽ ውሻ ከገጠመን የምንከላከልበትን በትር ይዞ፣ የሙልሙል ከረጢቱን ታጥቆ ተነሣ፡፡ ብርዱን ለመከላከል ሁላችንም ያለንን ሙቀት የሚሰጥ ልብስ ለበስን፡፡
ከተማችን ተፈሪ ኬላ፣በብርሃን እሣት ነድዳለች፡፡ ገና ችቦ ሲለኮስማ ጉድ ነው፡፡ በፊልም የምናውቃቸውን የአውሮፓ ከተሞች መምሰሏ የማይቀር ነው፡፡ ሻይ ቤቶች፣ ቡና ቤቶች፣ ጠላ ቤቶችና አረቄ ቤቶች በራሳቸው ሙዚቃ ናላቸው ዞሯል፡፡
እኔ ከረጢቴን ተቀበልኩ፡፡ ሣንቲምና ብር መያዣ እንዲሆነኝ የጂንስ ሱሪዬን ኪስ አመቻቸሁ፡፡ ይሄ ካነሰ የደረብኩት ጃኬት ኪስ አንድ ዶሮ መደበቅ ይችላል፡፡ ከተማው መሀል ላይ ካለችው የአድባር ዛፍ ሥር ከባህር ዛፍ እንጨት በተሠራው ቦታ ተቀምጠን ድምፃችንን ሳልን፣ አቅማችንን ሞከርን፡፡ የፈለቀ ድምጽ ዛሬ ብሶበታል፡፡
ቡሄ - ቡሄ በሉ
ል - ጆ- ች ሁሉ!
ቡሄ መጣ ያ - መላጣ
ቅቤ ቀቡት እንዳይነጣ!
ሁላችንም ለፈለቀ አጨበጨብንለት፡፡ ይህን ጭብጨባ ተከትሎ ግን ድንገት በቀለ ወደ እኛ ሲመጣ አየነው፡፡ የፈራሁት ደረሰ!
“የምን ድርቅና ነው - አንፈልግም ካልን ለምን ይመጣል?” አለኝ ዳኜ፤ወደ ጆሮዬ ተጠግቶ፡፡
“ምን ቸገረህ ይምጣና ይገተር፣ ሣንቲም እንደሆን አያገኛት!; አለ ሌላው፡፡
አጅሬው ቀጥ ብሎ መጣ፡፡ ቢሆንም ሁላችንም ፊት ነሣነው፡፡
መጀመሪያ ወይዘሮ አበበች ጠጅ ቤት ሄድን፡፡ መሀል ከተማ ነው፡፡ እትዬ አበቡ ዶቃ መልክ ያለውን የጠጅ ማንቆርቆሪያ ይዘው በፈገግታ ተቀበሉን፡፡ አጠር ያሉ፣ ደርባባ ሴት ወይዘሮ ናቸው፡፡ ትልልቅ ዓይኖቻቸውን እያበሩ፣ እኛ ደግሞ የአምፑሉን ብርሃን እየሸሸን ተፋጠጥን፡፡
“ይሄ የአበበ ልጅ አይደለም? ይሄ የእገሌ ልጅ አይደለም?” ሲሉ ግጥሙ ጠፋብን፡፡ ሣንቲም  እንደሚሰጡን ገምተን ነበር፡፡ ልክ የለበሷት ጋዋን ኪስ ውስጥ እጃቸውን ሲሰዱ ፈለቀ ግጥሙ መጣለት፡፡
   “ዓመት ዓውዳመት
ድገምና ዓመት፤
የእትዬ አቡን ቤት
ወርቅ ይዝነብበት!”   
…እያልን አስነካነው፡፡ በትራችን የሊሾውን ወለል እንዳይጐዳ አድርገን፣ ገና ሳንቲሙ ሳይሰጠን  ምርቃቱን አቀላጠፍነው፡፡ ማመን አቃተን፡፡ አሥር ብር አሻሩን። ኡ…ኡ…ኡ…ማለት ነው የቀረን። ቀወጥነው፡፡ እትዬ አበቡ በትልልቅ ዓይኖቻቸው አዩን፡፡ ከዚያ በኋላ ጋሽ በላይ ማንቆርቆሪያቸውን እንደያዙ መጡና አሥር ብር ጨመሩልን፡፡  ከሁላችንም የበለጠ የተደሰተው ዳኜ ነው። አባቱ ናቸው፡፡
ፉጨቱ አገር ሞላ፡፡ በቃ አሁን ጋሽ ሰብስቤን እንኳ ባናገኝ ግድ የለም፡፡ ወደ ሌላ ሰው ቤት  ስንሄድ በቀለ ከኋላችን ሲከተለን ነበር፡፡ ነገረ ሥራውን ፈጽሞ አልወደድነውም፡፡ እትዬ የውብዳር ቤት ነበር የሄድነው። የእሷ ግሮሠሪ ከተማው እንብርት ላይ ነው፡፡ ከሺኢቾ፣ ከሆንቾና ከባለወልድ የሚመጡ መንገዶች መገናኛ!
እዚያም ጨፈርን፡፡ እትዬ ውቤ መጣች፡፡ የከተማዋ ጣቢያ አዛዥም ብቅ አለ፡፡ ፊቱ እንደ ሮማን ከብልል ያለና ሙሉ ነው፡፡ ሞቅ ብሎታል። አፉን ያዝ እያደረገው፣ “ግጥሙን አስተካከሉ” አለን። ሁላችንም ዝም አልን፡፡
“እናቴ ቤት አለኝ ለከት
አክስቴ ቤት አለኝ ለከት” ነው የሚባለው፤የዛሬ ልጆች ዝም ብላችሁ ሣንቲም ብቻ! ወይኔ በኛ ጊዜ!” አለና ሁለት ብር አውጥቶ ሰጠን፡፡ እትዬ የውብዳር በፈገግታ ተሞልታ፤ “እናንተ በዚህ ጨለማ ውሻ እንዳይነክሳችሁ!..በጊዜ ግቡ!” አለችን፡፡ እኛ ግን ምክሯን አልነበረም የፈለግነው፡፡ ብሯን ነው፡፡ ወደ ባንኮኒዋ ስትሄድ የሁላችንም አይን ተከትሏት ነጐደ።
“በሉ በደንብ ጨፍሩ!” አለችን በሚያምር ፈገግታ። የሷን ስምና የልጅዋን ሥም እየጠራን አሞጋገስናት፡፡ አምስት ብር! የከበርቴነት ስሜት ተሠማን፡፡ ፈለቀ ድምፁ ጨመረ፡፡ እንደ ፏፏቴ አንቆረቆረው፡፡ ከረጢታችንን ሙልሙል ሞላው። ብሮቹን በጂንስ ኪሴ ውስጥ ጠቀጠቅኩ፡፡ ሁሉን አዳርሰን ስናበቃ፣ለክፍፍል ተቀመጥን። ያኔ ሁላችንም በሚደርሰን ገንዘብ የምንበላው የምንጠጣውን --- ለስላሳ… ብርቱካን… ብስኩት… በዓይነ ህሊናችን መሳል ጀመረን፡፡  
ከተማው በየቦታው በተለኮሰ ችቦ ውጋጋን ደምቋል፡፡ አበባ የሚመስሉ ነበልባሎች በየደጁ ፈክተዋል፡፡
እጄን ወደ ቀኝ ኪሴ ከተትኩ፡፡ ሁሉም አዩኝ። እኔም አየኋቸው፡፡ እንደገና እጄን ወደ ከረጢቱ ሰደድኩ፡፡ ዓይኔን ማመን አቃተኝ፡፡ ያገኘሁት ጠፍጣፋ ድንጋዮች ነበር፡፡
“እናንተ…እናንተ” አልኩና አዙሮኝ ወደቅሁ፡፡ ለካስ ኪሴ ቀዳዳ ነበር፡፡ አንድ ሁለቱ የቡሄ ጓደኞቼ ግን “በቀለ የሆነ ነገር አድርጐ ሲሮጥ አይተነዋል!” በማለት እሱ ወደሮጠበት አቅጣጫ አስነኩት፡፡ እኔ ከወደቅሁበት ስነሳ ከተማው በሙሉ የገሀነም እሣት ይመስል ነበር፡፡

Published in ልብ-ወለድ
Page 8 of 19