• በቅዱስ ዐማኑኤልና በአቡነ አረጋዊ አድባራት፤ አስተዳደሩና ሰበካ ጉባኤያት ተፋጠዋል
• ፓትርያርኩ የመሩበት ጥናታዊ ሪፖርት ለቋሚ ሲኖዶሱ ይኹንታ አለመቅረቡ አነጋጋሪ ኾኗል


    በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በርካታ አድባራት፣ የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በበላይነት ለመምራትና ለመቆጣጠር ሥልጣንና ተግባር ያላቸው የሰበካ መንፈሳዊ አስተዳደር ጉባኤ አባላት፣ በሙስናና ብልሹ አሠራር በሚታሙ የአስተዳደር ሓላፊዎች መታገዳቸው አደገኛ አዝማሚያ እየያዘ መምጣቱ ተገለጸ፡፡ ሀገረ ስብከቱም ተጣርተው በሚቀርቡለት ሪፖርቶች ላይ አፋጣኝ ውሳኔ አለመስጠቱ “ትክክለኛ መፍትሔ የማግኘት ተስፋችንን አዳክሞታል፤” ይላሉ ምእመናኑ፡፡ባለፉት ሦስት ወራት ለአዲስ አድማስ የደረሱ ጥቆማዎች እንደሚያስረዱት፤ የሰበካ ጉባኤያቱ ምክትል ሊቃነ መናብርት፣ ከሓላፊነት ይታገዳሉ አልያም በአስተዳደር ተግባር የመሳተፍ ድርሻቸው ተዳክሞ ደመወዝና ሥራ ማስኬጃ በመፈረም ብቻ ተወስኗል፡፡ ከአስተዳደሩ ሓላፊዎች የተለየ ሐሳብ የሚያነሡ የማኅበረ ካህናት ተወካዮች፤ ከሥራና ከደመወዝ ይታገዳሉ፤ ከፈቃዳቸው ውጭ ወደ ሌሎች አድባራት ዝውውር ይጠየቅባቸዋል፤ የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራንና የንብረት አመዘጋገብን አጥብቀው የሚቆጣጠሩ የማኅበረ ምእመናን ተወካዮች ከአባልነት ከመታገዳቸውም በላይ “ለማበጣበጥ እየሠሩ ነው፤ አሸባሪዎች ናቸው” በሚል ለመንግሥታዊ አስተዳደርና የፍትሕ አካላት ክሥ ይቀርብባቸዋል ተብሏል፡፡
በደብረ ከዋክብት አቡነ አረጋዊና ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን፣ አስተዳዳሪው፤ የሰበካ ጉባኤውን ውሳኔ እንደማይተገብሩ የጠቆሙ ምዕመናን፤ በምክትል ሊቀ መንበሩ የማይታወቁ የባንክ ሂሳቦችን በደብሩ ስም እንደሚያንቀሳቅሱ፣ አግባብነት የሌለው የሠራተኞች ዕድገትና ዝውውር እንደሚፈፅሙ ተናግረዋል፡፡
አስተዳዳሪው ቀደም ሲል የቤተ ክርስቲያንን መሬት ለግል ጥቅም በማዋላቸው ከሓላፊነት ታግደው እንደነበር ያስታወሱት ምእመናኑ፤ ደብሩ ለሀገረ ስብከቱ መክፈል የሚገባውን የኻያ ፐርሰንት ፈሰስ ሳይከፍሉ በመቅረታቸው ለዕዳ እንደዳረጉት ይናገራሉ፡፡ የሰበካ ጉባኤው አባላት፣ በማኅበረ ካህናቱ ተቀባይነት እንዳይኖራቸው በተወላጅነት እንደሚከፋፍሉና ካህናቱን ከደመወዝና ከሥራ በማገድ ለችግር እንደሚያጋልጧቸው ምዕመናኑ ይገልፃሉ፡፡
የአለመግባባቱ መንሥኤ፣ የሰበካ ጉባኤው አባላት የደብሩን ገቢና ወጪ አጥብቀው በመቆጣጠራቸውና የፋይናንስ ሪፖርት፤ በመጠየቃቸው እንደኾነ የሚገልጸው የክፍለ ከተማው ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ሪፖርት አባላቱ፣ ደመወዝ ፈርሞ ከማውጣት ውጭ በውሳኔ አሰጣጥ ረገድ በቃለ ዐዋዲው በተሰጣቸው ሥልጣንና ተግባር እየተሳተፉ እንዳልኾነ አረጋግጧል፡፡ የአስተዳዳሪውን አልታዘዝ ባይነት የሚገልጸው ሪፖርቱ፤ ለሀገረ ስብከቱ ማስተላለፉን ቢያውቁም ምንም ዐይነት ምላሽ አለመሰጠቱ ግራ እንዳጋባቸው - ምእመናኑ ይናገራሉ፡፡
በተመሳሳይ አኳኋን ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በቅርቡ ባካሔደው የሕንጻ እና የመሬት ኪራይ ተመን ጥናታዊ ሪፖርት ከበድ ባለ ሙስና የተተቸው የደብረ ገሊላ ቅዱስ ዐማኑኤል አስተዳደር፤ ከሙዳየ ምጽዋት ቆጠራና ከንብረት ሽያጭ ጋር በተያያዘ ከምእመናኑ ጋር ፍጥጫ ውስጥ ገብቷል፡፡ በየካቲት 2007 የተመረጠው ሰበካ ጉባኤ፣ የደብሩን የአሠራር ክፍተቶች በመቅረፍ ገቢውን በተሻለ መልኩ ለመቆጣጠርና ለማሳደግ ቢንቀሳቀስም አንድ የካህናት ተወካይ ከሥራና ከደመወዝ፣ ኹለት የምእመናን ተወካዮች ደግሞ ከአባልነት መታገዳቸው ውዝግቡን እንዳካረረው ተጠቅሷል፡፡
የቤተ ክርስቲያኒቱን ሀብትና ንብረት ለመጠበቅ ሲባል ካህናትና ምእመናን የሥራ ሓላፊነታቸውንና የቤተ ክርስቲያን ልጅነት ግዴታቸውን ለመወጣት በሚያደርጉት ጥረት ለሚፈጠርባቸው ዕንቅፋት ሀገረ ስብከቱ ሓላፊነት እንደሚወስድ ቢገልጽም ልኡካኑ ችግሩን ለመፍታት ባለመቻላቸው “ትክክለኛ መፍትሔ የማግኘት ተስፋችንን አዳክሞታል፤ ለሚደርሰው ማንኛውም ጥፋት ተጠያቂዎች አንኾንም” ሲሉ ምእመናኑ አሳስበዋል፡፡
በብሥራተ ገብርኤል፣ በካራ ቆሬ ፋኑኤል፣ በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም፣ በላፍቶ ቅዱስ ሚካኤል፣ በፉሪ ቅዱስ ገብርኤል፣ በደብረ ሲና እግዚአብሔር አብ፣ በሰሚት ቅ/ጊዮርጊስ፣ በሰሚት ኪዳነ ምሕረት፣ በሰሚት ቅ/ሩፋኤል፣ በጨፌ አያት ቅ/ገብርኤል፣ በአያት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ በፉሪ ቅ/ዑራኤል እና በሰሚት መድኃኔዓለም ከሰበካ ጉባኤ አባላት የሥራ ጊዜ መጠናቀቅ፣ የካህናትና ምእመናኑን ከአስተዳደሩ ጋር አለመግባባት ውዝግብ እንደፈጠረ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የሰበካ ጉባኤ አባላት በሥልጣናቸው አለመሥራት፣ የአስተዳደር ሓላፊዎች ብቃት ማነስ፣ ሙስና እና ብልሹ አሠራር እንዲኹም የስብከተ ወንጌል እንቅስቃሴ መዳከም በዐበይት መንሥኤነት ተዘርዝረዋል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ ቋሚ ሲኖዶሱ ይኹንታውን እንዲሰጥበት ፓትርያርኩ የመሩበትና ሙሰኛ የአድባራት ሓላፊዎች ምዝበራ በሕግ አግባብ እንዲታይ የሚጠይቀው የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ጥናታዊ ሪፖርትና ውሳኔ በአጀንዳነት አለመቅረቡ አነጋጋሪ ሆኗል ተባለ፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ አስፈጻሚ አካል የኾነውና በፓትርያርኩ ሊቀመንበርነት የሚመራው ቋሚ ሲኖዶሱ፣ በዚኽ ሳምንት መደበኛ ስብሰባው ይኹንታውን እንደሚሰጥበት ቢጠበቅም፤ የቅዱስ ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ የፓትርያርኩ ምሪት እንዳልደረሳቸው በመግለጻቸውና የተመራበት ሰነድም የትኛው አካል ጋር እንዳለ በስብሰባው ወቀት ባለመታወቁ በአጀንዳነት ሳይቀርብ መቅረቱን የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች ተናግረዋል፡፡
ዘግይቶ በደረሰን ዜና፣ ጥናታዊ ሪፖርቱና የውሳኔው ቃለ ጉባኤ ትላንት ከቀትር በኋላ ለብፁዕ ዋና ጸሐፊ አሁነ ሉቃስ ዘግይቶ በመድረሱ በቀጣይ ሳምንት ማክሰኞ በአጀንዳነት ቀርቦ ይኹንታ እና የአፈጻጸም አቅጣጫ የሰጥበታል ተብሎ እንደሚጠበቅ ምንጮቹ ጠቁመዋል፡፡

Published in ዜና

     ከአንድ ወር በፊት ኢትዮጵያን የጎበኙት የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በአዲስ አበባ በነበራቸው የሁለት ቀናት ቆይታ ለሆቴል 1.3 ሚ. ዶላር ማውጣታቸውን ዊክሊ ስታንዳርድ ድረገጽ ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡
ኦባማ እና አብረዋቸው የመጡ የደህንነትና የልኡካን ቡድን አባላት በአዲስ አበባ በሚገኙ አራት ሆቴሎች ማረፋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በሁለት ቀናት ቆይታቸው ለሆቴሎቹ በድምሩ 1.3 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር መከፈሉን ገልጿል፡፡የጉብኝቱ አዘጋጆች በመጀመሪያ ከሂልተን ሆቴል ጋር የ412ሺ 390 ዶላር ውል መፈጸማቸውንና በቀጣይም ከኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል ጋር የ246ሺ 877 ዶላር፣ ከካፒታል ሆቴልና ስፓ ጋር ደግሞ የ178ሺ 433 ዶላር ውል መፈጸማቸውን የጠቀሰው ዘገባው፤ በመጨረሻም ከሸራተን አዲስ ሆቴል ጋር የ488ሺ 141 ዶላር ስምምነት መፈጸማቸውን ጠቁሟል፡፡የልኡካን ቡድኑ አባል የሆነ አንድ የዋይት ሃውስ ፎቶ ግራፍ አንሺን እማኝነት በመጥቀስ ዘገባው እንዳለው፣ ኦባማ በሁለት ቀናት ቆይታቸው ያረፉት በሸራተን አዲስ ሆቴል እንደነበር መረጋገጡንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡

Published in ዜና

     በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ከሚገኙ የተለያዩ ትምህርት ቤቶች ከፍተኛ ነጥብ አምጥተው ዩኒቨርሲቲ ለገቡ ከ2 ሺ 500 በላይ ሴት ተማሪዎች ትላንት የሽኝት ፕሮግራም ተደረገ፡፡
“ዘር ኢትዮጵያ” በተባለ ድርጅት በአፍሪካ ህብረት አዳራሽ በተካሄደው ፕሮግራም፤ በተለያዩ የሥራ መስኮች ስኬታማ የሆኑ ሴቶች ለተማሪዎቹ ከህይወት ልምድና ተሞክሮአቸው አካፍለዋል፡፡
ሴት ተማሪዎቹ በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው የሚገጥሟቸውን በርካታ ችግሮችና መሰናክሎች በአሸናፊነት ለመወጣት የዓላማ ፅናት ሊኖራቸው እንደሚገባ የተነገራቸው ሲሆን ለዚህም ከወዲሁ ራሳቸውን ማዘጋጀት እንደሚኖርባቸው ምክር ተለግሰዋል፡፡ለወጣት ተማሪዎቹ የህይወት ልምድና ተሞክሮአቸውን ካጋሩ ስኬታማ ሴቶች መካከል የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የኢንፎርሜሽን ሲስተም ምክትል ፕሬዚዳንት ወ/ሮ መሊካ በድሪ፣ በመከላከያ ሚኒስቴር የስነ ምግባር መከታተያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ብ/ጄ ዘውዱ ኪሮስና  የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አዜብ ወርቁ ይጠቀሳሉ፡ሽኝት የተደረገላቸው ሴት ተማሪዎች በአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ በኩል የተመረጡ መሆናቸው ታውቋል፡፡
የፕሮግራሙ አዘጋጅ “ዘር ኢትዮጵያ”፤ አራት መቶ ሴትና አንድ መቶ ወንድ ተማሪዎችን በየወሩ 200 ብር ድጋፍ እያደረገ ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ የሚያበረታታ ሲሆን በቀጣዩ ዓመት ድጋፍ የሚደረግላቸውን ተማሪዎች ቁጥር ወደ  1000 ለማድረስ እቅድ መያዙ ተገልጿል፡፡  

Published in ዜና

     ወርሃ  ዊ ክፍያ  እያስከፈለ የሚያስተምራቸውን ህፃናት ተማሪዎች ከውጭ አገር የገንዘብ እርዳታ መለመኛ አድርጓቸዋል የተባለው ኮቢ አካዳሚ አገልግሎት እንዳይሰጥ ታገደ፡፡
ትምህርት ቤቱ ከወላጆች በወር እስከ 600 ብር እየተቀበለ የሚያስተምራቸውን ህፃናት ተማሪዎች ፎቶግራፍ ለዚሁ ተግባር በተከፈተው ድረ ገፁ ላይ ከአጫጭር መግለጫዎች ጋር በመለጠፍ ወላጆች ሳያውቁ ለልመና ተግባር ሲጠቀምባቸው እንደቆየ ባለፈው ሰኔ 20 ቀን 2007 ዓ.ም በወጣው አዲስ አድማስ ጋዜጣ መዘገቡ ይታወሳል፡፡
ወላጆችም ጉዳዩን ለአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 2 ትምህርት ፅ/ቤት ማመልከታቸው አይዘነጋም፡፡
የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮውም ሰሞኑን እንደገለፀው፤ ትምህርት ቤቱን ከመማር ማስተማር ስራው ያገደው ሲሆን በህግም ለመጠየቅ መዘጋጀቱ ታውቋል፡፡
የት/ቤቱ የቀድሞ ዳይሬክተር ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ ሥራቸውን በገዛ ፈቃዳቸው እንደለቀቁ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Published in ዜና

     በመዲናዋ ባሉ ክፍለ ከተሞች በተመረጡ 10 ወረዳዎች ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ዘመናዊ የሰፈሮቹ የአድራሻና አቅጣጫ መጠቆሚያ ስርአት ሊዘረጋላቸው እንደሆነ እያካሄደ መሆኑን የአዲስ አበባ አስተዳደር የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ አስታወቀ፡፡
የቢሮው የኮሙኒኬሽን የሥራ ሂደት መሪ አቶ ማርቆስ አለማየሁ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ ዝርጋታው አቅጣጫ ጠቋሚ ምልክቶችን፣ ብሎክና የቤት ቁጥር ታፔላዎችን ያካትታል፡፡ የአድራሻ ስርዓቱ በዋናነት ለፖስታ አገልግሎት፣ የእሳት አደጋ መኪኖች ፈጥነው እንዲደርሱ እንዲሁም የአምቡላንስ አገልግሎት ለማግኘትና ወንጀልን ለመከላከል ወሳኝ መሳሪያ ይሆናል ተብሏል፡፡
ስርአቱን ለመዘርጋትም ካርታ የማዘጋጀት ስራ ሲከናወን የቆየ ሲሆን ታፔላዎቹ ደረጃቸውን ጠብቀው እንዲመረቱ ከብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን፣ ከህብረት ማኑፋክቸሪንግ ማሽን ኢንዱስትሪ ጋር የ40 ሚሊየን ብር ውል መገባቱን የጠቆሙት አቶ ማርቆስ፤ አሁን የስራው የመጀመሪያ ምዕራፍ ወደ ሆነው ምልክት ተከላ ተሸጋግሮ ስራው እየተገባደደ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
ከአስሩም ክፍለ ከተሞች አንድ አንድ ወረዳ የተመረጠ ሲሆን ለአብነትም ጉለሌ ወረዳ 10፣ የካ ወረዳ 13፣ ቂርቆስ ወረዳ 2 እና አዲስ ከተማ ወረዳ 9ን ጠቅሰዋል፡፡ የእነዚህ ወረዳዎች ተከላ እንደተጠናቀቀም 30 የሚሆኑ ወረዳዎች ላይ ወደ ተግባር ለመግባት በዝግጅት ላይ ነን ብለዋል - የሥራ ሂደት መሪው፡፡

Published in ዜና

መንግስት ለአስቸኳይ እርዳታ 33 ሚ. ዶላርቢያሰባስብም፣ ተመድ 230 ሚ. ዶላር ያስፈልጋል ብሏል
• “አብዛኛው ተረጂ የሚገኘው በኦሮምያ ክልል ነው”

   የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኢትዮጵያ በተከሰተው የዝናብ እጥረት ሳቢያ የምግብ እህል እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ከዚህ በፊት ከተገመተው በላይ በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንና 4.5 ሚሊዮን መድረሱን አስታወቀ፡፡
አንድ ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣን በበኩላቸው፤ ችግሩን ለመፍታት ክልሎች ራሳቸው ከሚመድቡት በጀት በተጨማሪ መንግሥት 700 ሚ. ብር መድቦ ለተረጂዎች ድጋፍ ለማድረግ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ጠቅሰው ከተረጂዎች መካከል 40 በመቶ ያህሉ በኦሮምያ ክልል እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ያወጣውን ሪፖርት ጠቅሶ አጃንስ ፍራን ፕሬስ ትናንት እንደዘገበው፣ በአመቱ የዝናብ መጠኑ ከተገመተው በታች መሆኑን ተከትሎ የምግብ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ከተገመተው 2.9 ሚሊዮን የ55 በመቶ ጭማሪ በማሳየት 4.5 ሚሊዮን ደርሷል፡፡
በኢትዮጵያ የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ሃላፊ ዴቪድ ዴል ኮንቴ እንዳሉት፤ በዝናብ እጥረቱ ክፉኛ የተጎዱት የአገሪቱ አካባቢዎች ምስራቃዊ አፋርና ደቡባዊ ሶማሌ ክልሎች ሲሆኑ በአንዳንድ የኦሮምያ፣ የትግራይና የአማራ ክልሎች አካባቢዎችም፣ ባልተለመደ ሁኔታ የከብቶች ግጦሽና የውሃ ሃብቶች እጥረት ተከስቷል፡፡በአሜሪካ መንግስት የሚደገፈው “ፋሚን ኧርሊ ዋርኒንግ ሲስተምስ ኔትወርክ” የተባለ የርሃብ ቅድመ ማስጠንቀቂያ የሚሰጥ ተቋምም፤ በኢትዮጵያ በርካታ እንስሳት በመኖ እጥረት ተጠቂ ሊሆኑ እንደሚችሉ ማስጠንቀቁንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡የኢትዮጵያ መንግስት ለአስቸኳይ የምግብ እርዳታ 33 ሚሊዮን ዶላር አሰባስቧል ያለው ዘገባው፤ ይሄም ሆኖ ግን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ መንግስት በመጪዎቹ አራት ወራት ጊዜ ውስጥ 230 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልገው ማስታወቁን አመልክቷል፡፡የእርዳታ ሰጪ ድርጅቶች ሃላፊዎች ችግሩ በተከሰተባቸው አካባቢዎች ምግብ የማከፋፈሉ እንቅስቃሴ ፈጣን አለመሆኑ እንዳሳሰባቸው ጠቁሞ፣ ለዚህ ችግር መከሰት አስተዋጽኦ ካበረከቱ ጉዳዮች መካከልም በጅቡቲ ወደብ ያለው መጣበብ አንዱ ነው ብሏል፡፡

Published in ዜና

     የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ባለፉት አምስት ዓመታት ጠቅላላ ሀብቱን ወደ 303.6 ቢሊየን ብር ማሳደጉን ገለፀ፡፡ የባንኩ የኮሙኒኬሽን ስራ አስኪያጅ አቶ ኤፍሬም መኩሪያ እንደተናገሩት፤ ባንኩ ከአምስት ዓመታት በፊት የነበረው ሀብት 74.2 ቢሊየን ብር ነበር፡፡ በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም የባንኩ ገቢ ወደ 23 ቢሊየን ብር ማደጉንና ከታክስ በፊት 12.6 ቢሊየን ብር ትርፍ ማግኘቱ ተገልጿል፡፡ ባንኩ አሁን ካሉት 965 ቅርንጫፎች ውስጥ 754ቱ ባለፉት አምስት ዓመታት የተከፈቱ ሲሆን የባንኩ ደንበኞችም ቁጥር 10.7 ሚሊየን ደርሷል፡፡ የኤቲኤም ተጠቃሚዎቹ ቁጥር 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን የደረሰ ሲሆን በቀጣይም ዘመናዊ የባንኪንግ ስርአቶችን በመዘርጋትና የአገልግሎት አድማሱን በማስፋት፣ በ2025 በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለመሆን አልሞ እየሰራ እንደሚገኝ አቶ ኤፍሬም ተናግረዋል፡፡
የአገር ውስጥ ቅርንጫፎችን ከማስፋት በተጨማሪም በውጪ አገራት ቅርንጫፎችን ለመክፈት ጥናቶች በመጠናቀቅ ላይ እንደሆኑ ተገልጿል፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት ባንኩ ለትላልቅ አገራዊ ፕሮጀክቶች 322 ቢሊየን ብር ያቀረበ ሲሆን ይህም የእቅዱ 187 በመቶ እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ የባንኩ ተቀማጭ ገንዘብ መጠን ከሶስት እጥፍ በላይ ማደግና የውጪ ምንዛሪ ገቢው መሻሻል ከዕቅድ በላይ አፈፃፀም እንዲያስመዘግብ አስችሎታል ተብሏል፡፡አንጋፋው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአሁኑ ጊዜ 23 ሺህ የሚደርሱ ሰራተኞች በስሩ ያስተዳድራል፡፡

Published in ዜና

  ከስምንቱ የምእተ አመቱ የልማት ግቦች ወይም Millennium Development Goals መካከል የእናቶችን ጤና ማሻሻል በአምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡ ይህም በዋናነት የእናቶችን ሞት በግማሽ መቀነስ እንዲሁም የስነተዋልዶ ጤና አገልግሎቶችን ለሁሉም እናቶች ተደራሽ ማድረግ ላይ ያተኩራል፡፡ የቤተሰብ እቅድ አገልግሎትን በተገቢው መንግድ ተደራሽ ማድረግ እና ሁሉም እናቶች የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች እንዲሆኑ ማድረግም በዚሁ እቅድ ስር የሚካተት ነው፡፡
የተለያዩ የእግዝና መከላከያ ዘዴዎችን መጠቀም የቤተሰብን ቁጥር ከመመጠን ባለፈ በአሁኑ ሰአት እጅግ አሳሳሲ ከሚባሉት የማህበረሰብ ጤና ችግሮች አንዱ የሆነውን የእናቶችን ሞት በእጅጉ ለመቀነስ ያስችላል። ለዚህም በየአመቱ ፅንስ በማቋረጥ ሳቢያ ህይወታቸውን የሚያጡ ቁጥራቸው በርካታ የሆኑ ሴቶችን እንደምሳሌ ማንሳት ይቻላል፡፡
ለዚህ ነው የተለያዩ የእርግዝና መከላከያ ምርቶች በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የእናቶችን ጤና በመጠበቅ እረገድ የሚኖራቸው አስተዋፅኦ ከፍተኛ ነው የሚባለው፡፡
በአለማችን ላይ ያለው የእርግዝና መከላከያ ምርቶች ተጠቃሚ ቁጥር ከግዜ ወደ ግዜ እየጨመረ መምጣቱን የአለም የጤና ድርጅት በግንቦት ወር 2015 ያወጣው መረጃ ያሳያል፡፡ በዚህም የእስያ እና የላቲን አሜሪካ ሀገራት ከፍተኛውን ድርሻ ሲይዙ ከሰራ በታች ያሉት የአፍሪካ ሀገራት ደግሞ በተቃራኒው በዚህ እረገድ ያላቸው ተጠቃሚነት እጅግ ዝቅተኛ የሚባል እንደሆነም መረጃው ይጠቁማል፡፡
በአጠቃላይ ግን አለምአቀፍ ደረጃ ያለው የዘመናዊ የእርግዝና መከላከያ ምርቶች አጠቃቀም ላይ ከግዜ ወደ ግዜ መሻሻሎች እንደታዩ ለዚህም እንደማሳያ የሚጠቀሰው በፈረንጆቹ 1990 53% የነበረው የተጠቃሚዎች ቁጥር በ2014 ወደ 57.4% ማደጉ እንደሆነም በመረጃው ተጠቅሷል፡፡
በፈረንጆቹ ከ2008-2014 ባለው ግዜ ውስጥም እድሜያቸው ከ15-49 የሆኑ የዘመናዊ የእርግዝና መቆጣጠሪያ ተጠቃሚ የሆኑ ሴቶች ቁጥር በእጅጉ እንደጨመረ እና በአህጉራችን አፍሪካም ከ23.6% ወደ 27.6% ማደጉን ይህ በያዝነው በፈረንጆቹ 2015 የወጣው መረጃ ያሳያል፡፡
አሁን ያለንበት የሀያአንደኛው ክፍለ ዘመን ብዙ ለውጦችን እያስተናገድን ያለንበት ዘመን እንደሆነ በተደጋጋሚ ሲነገር ይሰማል፡፡ ይህም ቀደም ሲል በስራችን ወይም በእለት ተእለት እንቅስቃሴያችን ውስጥ እንጠቀምባቸው የነበሩ ነገሮች በአዳዲስ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ተተክተው አንዳንዶቹም በፊት በነበረው ላይ እሴት ተጨምሮባቸው የሚስተዋሉ በመሆኑ ነው፡፡ በሁሉም የሙያ ዘርፎች ሊባል በሚችል ደረጃም አዳዲስ አሰራሮች እና የቴክኖሎጂ ውጤቶች ታይተዋል፡፡ ግዜው ካዘመነልን ነገሮች መካከል ያልተፈለገ እርግዝናል ለመከላከል የሚያስችሉ የተለያዩ የወሊድ መከላከያ ምርቶች ይጠቀሳሉ፡፡
ገነት ዳንኤል በሃያዎቹ መጨረሻ ላይ የምትገኝ ባለትዳር እና የሁለት ልጆች እናት ነች፡፡ ለስራ ጉዳይ ወደ አንድ በከተማችን የሚገኝ የግል ሆስፒታል በሄድኩበት ወቅት ነበር የገኘኋት፡፡ በቅድሚያ ነዋሪነቷ በሀዋሳ ከተማ 06 ቀበሌ እንደሆነ እና አዲስ አበባ የመጣችው ለህክምና መሆኑን አጫወተችኝ፡፡ የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት ተጠቃሚ መሆኗን ጠይቄ ከተረዳሁ በኋላ የትኛውን የወሊድ መከላከያ እንደምትጠቀም ጠየኳት...
“...በአሁኑ ሰአት በገበያ ላይ ለአጭር ወይም ለእረዥም ግዜ የሚሆኑ በጣም ብዙ የወሊድ መከላከያ አማራጮች አሉ ...እኔ ግን የምጠቀመው ቋሚ የእርግዝና መከላከያ ነው። እንደነገርኩሽ ሁለት ልጆች አሉኝ ...እና እነሱን በሚገባ ተንከባክቤ ማሳደግ እፈልጋለሁ፡፡ ስለዚህ ከባለቤቴ ጋር ተነጋግረን ባለሙያም አማክረን የወሰነው ነገር ነው፡፡...”
የፅሁፌ መነሻ ሀሳብ በአሁኑ ወቅት በሀገራችን የዘመናዊ የእርግዝና መከላከያ ምርቶች ላይ ያለውን መሻሻል ከተጠቃሚዎች አንደበት ለመስማት ነውእና ቀጣይ ጥያቄዬ በዘመናዊ የእርግዝና መከላከያ ምርቶች ላይ ያለውን መሻሻል እንዴት ታይዋለሽ? የሚል ነበር፡፡
“...በእኔ እይታ... በጣም ትልቅ ለውጥ ነው የመጣው ብዬ አስባለሁ፡፡ ምክንያቱም በፊት ግዜ ገበያው ላይ የነበሩት የወሊድ መከላከያ መድሀኒቶች በጣም ውስን እና ተመሳሳይ ናቸው፡፡ አሁን ላይ ግን አማራጩ በጣም ሰፊ ነው፡፡ ...ለምሳሌ እኔ የመጀመሪያ ልጄን ከወለድኩ በኋላ የምታጠባ እናት የምትወስደውን ነበር የምጠቀመው፡፡... በእንክብል የሚወሰዱ፣ በክንድ ላይ ተቀብረው እስከ አራት ወይም አምስት አመት እርግዝናን ለመከላከል የሚያስችሉ ሌሎችም ብዙ አማራጮች ቀርበውልናል፡፡ ...አሁን አንዲት ሴት ተገዳ ብትደፈር ወይም ጥንቃቄ የጎደለው ወሲብ ፈፅማ ቢሆን እርግዝና እንዳይፈጠር የሚያደርግ በ72 ሰአት ውስጥ የሚወሰድ መድሀኒትም አለ፡፡ ስለዚህ ከድሮው ጋር ስናወዳድረው አማራጩ በጣም ብዙ ነው... እና አሁን ላይ ያለን ሴቶች በጣም እድለኞች እንደሆንን ይሰማኛል...”  
ሌላዋ እናት ሉአም ትባላለች፡፡ የአንድ ወንድ ልጅ እናት የሆነችው ሉአምም የአጭር ግዜ የወሊድ መከላከያ ተጠቃሚ ነች፡፡ በአሁኑ ሰአት በሀገራችን ያለው የዘመናዊ የቤተሰብ እቅድ አገልግሎት ላይ ብዙ መሻሻሎች መታየታቸውን እና አቅርቦቱም ጥሩ የሚባል እንደሆነ ትናገራለች፡፡  
“...አሁን ያለው ሁኔታ ከድሮው ጋር በጣም ልዩነት አለው፡፡ ...ድሮ እናቶቻችን ወሊድን የሚቆጣጠሩት በባህላዊ መንገድ ከዛም በኋላ በጣም ጥቂት በሚባሉ የወሊድ መቆጣጠሪያ መድሀኒቶች ነው፡፡ አሁን ግን በጣም ብዙ አይነት የወሊድ መቆጣጠሪያ መድሀኒቶች አሉ፡፡ ልክ እንደ ብዛታቸው ሁሉ አይነታቸውም አጠቃቀማቸውም የተለያየ ነው፡፡ ስለዚህ አሁን ላይ ከእኛ የሚጠበቀው መርጦ መጠቀም ብቻ ነው፡፡...”
በሀገራችን የተለያዩ የቤተሰብ እቅድ አገልግሎቶችን ወይም ያልተፈለገ እርግዝናን ለመከላከል የሚያችስችሉ ምርቶችን ለተጠቃሚዎች በማድረስ ላይ የሚገኙ ሀገር በቀል እንዲሁም አለም አቀፍ ድርጅቶች አሉ፡፡ በዚህ ስራ ላይ ከተሰማሩት  አለምአቀፍ ድርጅቶች መካከል ዲኬቲ ኢትዮጵያ አንዱ ነው፡፡
ዲኬቲ ኢትዮጵያ በሀገራችን አገልግሎት መስጠት ከጀመረበት በፈረንጆቹ 1990 ጀምሮ በዘርፉ በርካታ ስራዎች መሰራታቸውን እና ህብረተሰቡን የዘመናዊ የቤተሰብ እቅድ አገልግሎት ተጠቃሚ ማድረግ እንደተቻለ በዲኬቲ ኢትዮጵያ ቴክኒካል ዲፓርትመንት ውስጥ በስራ ላይ የሚገኙት አቶ ሙሉጌታ አስጨናቂ ይናገራሉ፡፡
“...ዲኬቲ ኢትዮጵያ እንደሚታወቀው መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ መስራት ከጀመረበት በፈረንጆቹ አቆጣጠር 1990 አመተምህረት ጀምሮ በዘርፉ በርካታ ስራዎችን ስንሰራ 25 አመታትን አስቆጥረናል። ...ዲኬቲ ኢትዮጵያ ከሚሰራቸው ስራዎች ውስጥ አንዱ እና ዋናው የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት ላይ ሊውሉ የሚችሉ መድሀኒቶችን ወደ ሀገር ውስጥ ማስገባት ነው፡፡ ...እንደሚታወቀው የፕሮግራሙ ዋና ባለቤት የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ነው፡፡ እኛ ደግሞ አገልግሎቱ ተደራሽ ያልሆነባቸው ቦታዎች ላይ በመድረስ እንደ አንድ አጋር ሆነን የመንግስትን ፕሮግራም በማገዝ ላይ እንገኛለን፡፡ ስለዚህ ዲኬቲ በሀገራችን ውስጥ ያለው የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት ሽፋን እንዲጨምር ወይም እንዲሻሻላ የበኩሉን አስተዋፅኦ እያደረገ ያለ ድርጅት ነው፡፡...”
በአሁኑ ሰአት በርካታ የቤተሰብ እቅድ አገልግሎት አማራጮች በተለያየ መንገድ ለተጠቃሚዎች ቀርበዋል፡፡ ለመሆኑ እነዚህ አማራጮች የትኞቹ ናቸው? አቶ ሙሉጌታ ለዚህ ምላሽ አላቸው፡፡
“...እነዚህን የወሊድ መቆጣጠሪያ ምርቶች በሁለት ከፍለን ማየት እንችላለን፡፡ አንደኛው ጥምር የወሊድ መከላከያ የምንለው ነው፡፡ ...እነዚህ ጥምር ወይም (Combined oral contraceptives) የምንላቸው መድሀኒቶች በሁለቱ ማለትም ኤስትሮጅን እና ፕሮጀስትሮን በተባሉት ሆርሞኖች መልክ ሰው ሰራሽ በሆነ መልክ የሚሰሩ መድሀኒቶች ናቸው፡፡ ...ሁለተኛው አይነት ደግሞ Mono ወይም ነጠላ የምንላቸው መድሀኒቶች ናቸው፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ወርሀዊ የሆኑ በእንክብል መልክ የሚወሰዱ እንዲሁም በመርፌም የሚሰጡም አሉ፡፡ ...ለምሳሌ ኮንፊደንስ የምንለው በየሶስት ወሩ በመርፌ የሚሰጥ መድሀኒት አለ፡፡ ሌላ ደግሞ በ72 ሰአት ውስጥ የሚወሰድ Postpill የተባለ የድንገተኛ እርግዝና መከላከያ መድሀኒትም አለ፡፡ ...በተጨማሪም በአምስት  የተለያየ ቃና የተዘጋጁ ኮንዶሞች አሉ፡፡ ኮንዶም ጠቀሜታው ሁለት ነው፡፡ አንድም ያልተፈለገ እርግዝና እንዳይፈጠር ያደርጋል በሌላበኩል ደግሞ የኤች አይቪ ቫይረስ እንዳይተላለፍ ያደርጋል፡፡ ስለዚህ እነዚህ ለተወሰነ ግዜ እርግዝናን ለመከላከል የሚያስችሉ መድሀኒቶች ናቸው።...”እነዚህ ዘመናዊ የእርግዝና መከላከያ ምርቶች እርግዝናን በግዜያዊነት ለመከላከል የሚያስችሉ ሲሆኑ ማርገዝ በሚፈለግበት ግዜ መድሀኒቶቹን በማቆም ብቻ እርግዝና እንዲፈጠር ማድረግ ይቻላል፡፡ ግዜያዊ መባላቸውም በዚሁ መነሻነት እንደሆነ አቶ ሙሉጌታ ይገልፃሉ፡፡  
ሌላኛው አማራጭ እርግዝናን በቋሚነት ለመከላከል የሚያስችሉ ቋሚ የእርግዝና መከላከያ ዘዴዎች ናቸው። እነዚህ መድሀኒቶች ጭርሱን እርግዝና እንዳይፈጠር የሚያደርጉ ሲሆን ተጠቃሚዎች ይህን አይነት መድሀኒቶችን ከመውሰዳቸው በፊት በቂ የባለሙያ ምክር ማግኘት እንደሚኖርባቸውም ይናገራሉ፡፡
እነዚህ በርካታ አማራጮች መብዛታቸው የህብረተሰቡን መርጦ የመጠቀም እድል እንዲሰፋ እና የቤተሰብ እቅድ አገልግሎት ተጠቃሚዎችን ቁጥርም እንዲጨምር ያደርጋል ይላሉ፡፡   
“...በሀገራችን ደረጃ የተለያዩ የወሊድ መከላከያ ዘዴዎችን እያበዛን በመጣን ቁጥር ተጠቃሚዎች የሚፈልጉትን እና ከጤናቸው ጋር የሚስማማውን ዘዴ መርጠው የመጠቀም እድላቸው በጣም ይሰፋል፡፡ በተመሳሳይ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ቁጥርም እየጨመረ ይሄዳል፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ...በሀገሪቷ ውስጥ ያለው የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት ሽፋን ከፍ እያለ ይመጣል፡፡ ...ዛሬ እድሜ ለቴክኖሎጂ ብዙ አይነት አማራጮች ቀርበዋል፡፡ ተጠቃሚዎችም ከድሮ የተሸለ ግንዛቤ አላቸው፡፡ ...ይህ ትልቅ እመርታ ነው፡፡...”
እዚህ ላይ ሊስተዋል የሚገባው ይላሉ አቶ ሙሉጌታ፡-
“...እዚህ ላይ ሊስተዋል የሚገባው ሁሉም የቤተሰበ ምጣኔ አገልግሎት ተጠቃሚዎች የትኛውንም አይነት መድኒት ከመውሰዳቸው አስቀድሞ የባለሙያ ምክር እና እገዛ ማግኘት ይኖርባቸዋል፡፡...”

Published in ላንተና ላንቺ

15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በቤጂንግ ከተማ የወፍ ጎጆ ስታድዬም ዛሬ ይጀመራል፡፡  የመክፈቻው ውድድር የመጀመርያው የወርቅ ሜዳልያ የሚሸለምበት የወንዶች ማራቶን ነው፡፡ ኬንያ ባለፉት ሁለት ዓመታት ሁለት የማራቶን ሪከርድ የሰበሩ አትሌቶችን በማሳተፏ ከፍተኛ ግምቱን ትወስዳለች፡፡ ተቀናቃኛቸው የዓለም ሻምፒዮና የብር ሜዳልያ የወሰደው ሌሊሳ ዴሲሳ ነው፡፡ ከዚህ በታች ኢትዮጵያ ባለፉት 14 የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች ያስመዘገበችውን ስኬት ዳስሰናል፡፡     
               ክፍል - 2
     15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በቤጂንግ ከተማ የወፍ ጎጆ ስታድዬም ዛሬ ይጀመራል፡፡  የመክፈቻው ውድድር የመጀመርያው የወርቅ ሜዳልያ የሚሸለምበት የወንዶች ማራቶን ነው፡፡ ኬንያ ባለፉት ሁለት ዓመታት ሁለት የማራቶን ሪከርድ የሰበሩ አትሌቶችን በማሳተፏ ከፍተኛ ግምቱን ትወስዳለች፡፡ ተቀናቃኛቸው የዓለም ሻምፒዮና የብር ሜዳልያ የወሰደው ሌሊሳ ዴሲሳ ነው፡፡
ከዚህ በታች ኢትዮጵያ ባለፉት 14 የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች ያስመዘገበችውን ስኬት ዳስሰናል፡፡
በ1500 ሜ
1 የብር ሜዳልያ በወንዶች
1 የነሐስ ሜዳልያ በሴቶች
ኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ1500 ሜትር በሁለቱም ፆታዎች የወርቅ ሜዳልያ ስኬት የላትም፡፡ በሴቶች 1500 ሜትር  በ1999 እ.ኤ.አ ሜዳልያ በቁጥሬ ዱለቻ ሲገኝ፤  በወንዶች ግን ብቸኛውን ውጤት በ2009 እኤአ በርሊን ላይ ደረሰ መኮንን በብር ሜዳልያ አስመዝግቧል፡፡
በ3ሺ መሰናክል 1 የነሐስ ሜዳልያ በሴቶች
በ3ሺ መሰናክልም በሁለቱም ፆታዎች አሁንም ለኢትዮጵያ የወርቅ የሜዳልያ ውጤት ተመዝግቦ አያውቅም፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት በሞስኮው 14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በሴቶች ግን ሜዳልያዎች ተገኝተዋል፡፡ ያመዘገቧቸው የብር እና የነሐስ ሜዳልያዎች ናቸው፡፡
በ800 ሜትር 1 የወርቅ ሜዳልያ በወንዶች
በ800 ሜትር የኢትዮጵያ አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች ያን ያህል ተፎካካሪዎች አይደሉም፡፡ በወንዶች የመጀመርያው የወርቅ ሜዳልያ ድል የተመዘገበው ከሁለት ዓመት በፊት በመሃመድ አማን ነበር፡፡
በ5ሺ ሜትር
4 የወርቅ፣ 1 የብርና 6 የነሐስ ሜዳልያዎች በሴቶች
 1 የወርቅ፣ 2 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎች በወንዶች
በ5ሺ ሜትር ሴቶች ፍፁም የበላይነት የነበራት ኢትዮጵያ የወርቅ እና የብር ሜዳልያዎች ሳታገኝ ሁለት የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች ካለፉ በኋላ ከ2 ዓመት በፊት ሞስኮ ላይ በሴቶች የወርቅ እና የነሐስ እንዲሁም በወንዶች ተጨማሪ ነሐስ በማግኘት ወደ ውጤት ተመልሳለች፡፡
 በ5ሺ ሜትር ሴቶች በዓለም ሻምፒዮና ከወንዶች እጅግ የላቀ ውጤት አላቸው፡፡ በ14 የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች ኢትዮጵያ በነበራት የተሳትፎ ታሪክ በ5ሺ ሜትር ሴቶች  4 የወርቅ ፤ 1 የብርና 6 የነሐስ ሜዳልያዎችን ሰብስባለች፡፡ በ1999 እና በ2001 እኤአ ላይ በተደረጉት ሁለት ተከታታይ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች አየለች ወርቁ ሁለት የነሐስ ሜዳልያዎችን በማግኘት ፈርቀዳጅ ነበረች፡፡ ከዚያም በ2003 እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፤ በ2005 እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፣ መሰረት ደፋር የብር እንዲሁም እጅጋየሁ ዲባባ የነሐስ፤ በ2007 እኤአ መሰረት ደፋር የወርቅ፤ በ2009 እና በ2011 እኤአ መሰረት ደፋር ሁለት የነሐስ ሜዳልያዎችን በርቀቱ አግኝተዋል፡፡  በ2013 እኤአ ላይ ደግሞ መሰረት ደፋር የወርቅ እንዲሁም አልማዝ አያና የነሐስ ሜዳልያዎችን ማግኘት ችለዋል፡፡
በወንዶች 5ሺ ሜትር በሻምፒዮናው ታሪክ ከአንድ ጊዜ በላይ የወርቅ ሜዳልያውን ለማግኘት ለኢትዮጵያ አትሌቶች ፈተና ሆኖ ቆይቷል፡፡ለኢትዮጵያ የመጀመርያው የሜዳልያ ውጤት የተመዘገበው በ1991 እኤአ ላይ በፊጣ ባይሳ በተገኘው የብር ሜዳልያ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ በ1993 እኤአ ላይ ሃይሌ ገብረስላሴ የብርና ፊጣ ባይሳ የነሐስ፤ በ2001 እኤአ ላይ ሚሊዮን ወልዴ የብር፤በ2003 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ የነሐስ፤ በ2005 እኤአ ላይ ስለሺ ስህን የብር፤ በ2009 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ የወርቅ እንዲሁም በ2011 እኤአ ላይ ደጀን ገብረመስቀል እንዲሁም በ2013 እኤአ ደጀን ገብረመስቀል  የነሐስ ሜዳልያዎችን ወስደዋል፡፡ በአጠቃላይ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ5ሺ ሜትር ወንዶች በኢትዮጵያ አትሌቶች የተመዘገበው ውጤት ከሴቶቹ ያነሰ ሲሆን 1 የወርቅ፤ ሁለት የብርና ሶስት የነሐስ ሜዳልያዎች ናቸው፡፡
በ10ሺ ሜትር
9 የወርቅ፣ 5 የብርና 4 የነሐስ ሜዳልያዎች  በወንዶች
 6 የወርቅ፣ 5 የብርና 4 የነሐስ  ሜዳልያዎች በሴቶች
በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ የበላይነት ካልተነቀነቀባቸው የውድድር ርቀቶች ዋንኛው 10ሺ ሜትር ነው፡፡ ከ1983 እኤአ ጀምሮ በተካሄዱ 14 የዓለም ሻምፒዮናዎች ኢትዮጵያ 9 የወርቅ ሜዳልያ በወንዶች እንዲሁም 6 የወርቅ ሜዳልያ በሴቶች በማግኘት ተሳክቶላታል፡፡ በዓለም ሻምፒዮና ላይ በ10ሺ ሜትር ወንዶች የመጀመርያው የሜዳልያ ድል የተመዘገበው በ1993 እኤአ በኃይሌ ገብረስላሴ በተገኘው የወርቅ ሜዳልያ ነበር፡፡ ከዚያም በኋላ በ1995፣ በ1997 እና በ1999 እኤአ ላይ ሶስት የወርቅ ሜዳልያዎችን አከታትሎ የተጎናፀፈውም ራሱ ኃይሌ ገብረስላሴ ነበር፡፡ በ1999 እኤአ ላይ አሰፋ መዝገቡ ተጨማሪ የብር ሜዳልያ ወስዷል፡፡ በ2001 እኤአ ላይ አሰፋ መዝገቡ የብርና ኃይሌ ገብረስላሴ የነሐስ፤ በ2003 እኤአ ቀነኒሳ በቀለ የወርቅ፣ ኃይሌ ገብረስላሴ የብርና ስለሺ ስህን የነሐስ፤ በ2005 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ የወርቅ እና ስለሺ ስህን የብር፤ በ2009 እኤአ ቀነኒሳ የወርቅ እንዲሁም በ2011 እኤአ ላይ ኢብራሂም ጄይላን የወርቅ እና ኢማና መርጋ የነሐስ ሜዳልያዎችን እንዲሁም በ2013 እኤአ ኢብራሂም ጄይላን የብርና ኢማና መርጋ የነሐስ ሜዳልያዎች በመሰብሰብ የኢትዮጵያን የበላይነት ለረጅም ጊዜ አስጠብቀዋል፡፡ በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ በ10 ሺ ሜትር ወንዶች 9 የወርቅ፣ 5 የብርና 5 የነሐስ ሜዳልያዎችን ሰብስባለች ማለት ነው፡፡ በ2013 እኤአ የወርቅ ሜዳልያውን ከኢትዮጵያ የነጠቀው ሞፋራህ ነው፡፡
በሌላ በኩል በ10ሺ ሜትር ሴቶች በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ የመጀመርያው የሜዳልያ ድል የተመዘገበው በ1995 እኤአ ደራርቱ ቱሉ በተጎናፀፈችው የብር ሜዳልያ ነበር፡፡ በ1999 እኤአ ላይ ጌጤ ዋሚ የወርቅ፤ በ2001 እኤአ ደራርቱ ቱሉ የወርቅ፣ ብርሃኔ አደሬ የብር እና ጌጤ ዋሚ የነሐስ፤ በ2003 እኤአ ብርሃኔ አደሬ የወርቅ እና ወርቅነሽ ኪዳኔ የብር፤ በ2005 እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፣ ብርሃኔ አደሬ የብር እና እጅጋየሁ ዲባባ የነሐስ፤ በ2007እኤአ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ፤ በ2009እኤአ መሰለች መልካሙ የብርና ዉዴ አያሌው የነሐስ ሜዳልያዎች አግኝተዋል። በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ በ10 ሺ ሜትር ከ4 አመት በፊት ምንም አይነት የሜዳልያ ውጤት ባይኖራትም በ2013 እኤአ ላይ ጥሩነሽ ዲባባ የወርቅ ሜዳልያ በመውሰድ ክብሩን መልሳለች፡፡ በላይነሽ ኦልጅራ ደግሞ የነሐስ ሜዳልያ ተጐናፅፋለች። በአጠቃላይ ባለፉት 14 የዓለም ሻምፒዮናዎች በሴቶች 10ሺ ሜትር 6 የወርቅ፣ 5 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎችን አግኝታለች፡፡
በማራቶን
1 የወርቅ፣ 2 የብር፣ 3 የነሐስ ሜዳልያዎች በወንዶች
 1 የነሐስ ሜዳልያ በሴቶች  
ኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ በማራቶን ውድድር በሁለቱም ፆታዎች ከ1 በላይ የወርቅ ሜዳልያ አግኝታ አታውቅም፡፡ በወንዶች ማራቶን ኢትዮጵያ የመጀመርያ የሜዳልያ ድሏን በመጀመርያው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ1983 እኤአ ላይ ያገኘችው ከበደ ባልቻ ባስመዘገበው የብር ሜዳልያ ነበር። ከዚያ በኋላ በ2001 እኤአ ላይ ገዛሐኝ አበራ ብቸኛውን የወርቅ ሜዳልያ ድል አስመዘገበ፡፡ በ2009 እኤአ በፀጋዬ ከበደ እንዲሁም በ2011 እኤአ በፈይሳ ሌሊሳ በ2013 እ.ኤ.አ ደግሞ በታደሰ ቶላ ሦስት የነሐስ ሜዳልያዎች ተገኝቷል፡፡ እንዲሁም በ2013 እኤአ ሌሊሳ ዴሲሳ የብር ሜዳልያ አግኝቷል፡፡
በሴቶች ማራቶን ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮናው ያስመዘገበችው ብቸኛው የሜዳልያ ድል በ2009 እኤአ ላይ አሰለፈች መርጊያ ያስመዘገበችው የነሐስ ሜዳልያ ብቻ ነው፡፡
የምንገዜም የሜዳልያ ስብስብ ደረጃ
በ14 የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች የሰበሰበቻቸውን ሜዳልያዎች 300 (138 የወርቅ፤ 88 የብርና 74 የነሐስ) ያደረሰችው አሜሪካ አንደኛነቷን እንዳስጠበቀች ናት፡፡ ራሽያ 168 ሜዳልያዎች (53 የወርቅ፤ 60 የብርና 55 የነሐስ)፤ ኬንያ 112 ሜዳልያዎች (43 የወርቅ፤ 37 የብርና 32 የነሐስ)፤ ጀርመን 101 ሜዳልያዎች (35 የወርቅ፤ 28 የብርና 38 የነሐስ)፤ ጃማይካ 98 ሜዳልያዎች (24 የወርቅ፤ 42 የብርና 32 የነሐስ)፤ ሶቭዬት ህበረት 75 ሜዳልያዎች (22 የወርቅ፤ 25 የብርና 28 የነሐስ) እንዲሁም ኢትዮጵያ 64 ሜዳልያዎች (22 የወርቅ፤ 19 የብርና 23 የነሐስ) በ14 የዓለም ሻምፒዮናዎች የተሳትፎ ታሪካቸው በማስመዝገብ እስከ 7 ያለውን ደረጃ አከታትለው ይዘዋል፡፡
ባለብዙ ሜዳልያዎች ከኢትዮጵያ
በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ታሪክ የኢትዮጵያን ትልቅ ውጤት ያስመዘገበው አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ሲሆን 7 ሜዳልያዎችን (4 የወርቅ፤ ሁለት የብር እና 1 የነሐስ) በመሰብሰብ ነው፡፡ ይህ የኃይሌ ወጤት በከፍተኛ የሜዳልያ ስብስብ ከዓለም 4ኛ ከኢትዮጵያ አንደኛ ሆኖ ተመዝግቧል፡፡ ቀነነኒሳ በቀለ በ6 ሜዳልያዎች (5 የወርቅ እና 1 የነሐስ) በማስመዝገብ ከዓለም 6ኛ ከኢትዮጵያ 2ኛ ነው፡፡
በሴቶች የረጅም ርቀት ንግስቷና የአምስትና አስር ሺ ሜትር የዓለም ክብረወሰን ባለቤቷ ጥሩነሽ ዲባባ በዓለም ሻምፒዮና መድረክ አምስት የወርቅ ሜዳሊያ ያጠለቀች አትሌት ናት፡፡
ኢትዮጵያዊ የዓለም ሻምፒዮና ሪከርዶች
በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በኢትዮጵያውያን ተይዘው የሚገኙ ሶስት የዓለም ሻምፒዮና ሪከርዶች አሉ። የመጀመርያው በ2003 እኤአ ላይ በ9ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በ10ሺ ሜትር ብርሃኔ አደሬ የወርቅ ሜዳልያ ስታገኝ በ30 ደቂቃ ከ04.15 ሴኮንዶች ያስመዘገበችው ነው፡፡ ሁለተኛው በ2005 እኤአ በ10ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ5ሺ ሜትር ጥሩነሽ ዲባባ አሸንፋ የወርቅ ሜዳልያ ስትወስድ በ14 ደቂቃ ከ38.59 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ያስመዘገበችው ነው፡፡ 3ኛው ደግሞ በ2011 እኤአ በ12ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ10ሺ ሜትር ቀነኒሳ በቀለ የወርቅ ሜዳልያ ሲጎናፀፍ 26 ደቂቃ ከ46.31 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ያስመዘገበው ነው፡
በ14 የዓለም ሻምፒዮናዎች ኢትዮጵያ ከዓለም
ኢትዮጵያ ከ1983 እኤአ ጀምሮ በተካሄዱት 14 የዓለም ሻምፒዮናዎች በነበራት የተሳትፎ ታሪክ ሜዳልያ ሳታገኝ የቀረችው ውድድሩ 2ኛው የዓለም አትሌቲስ ሻምፒዮና በ1987 እኤአ በተካሄደበት ወቅት ብቻ ነበር፡፡ በ1983 እኤአ ላይ በ1ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሄልሲንኪ ፊንላንድ ላይ በ1 የብር ሜዳልያ ከዓለም 15ኛ፤ በ1991 እኤአ በ3ኛው ስቱትጋርት ጀርመን ላይ በ1 የብር ሜዳልያ ከዓለም 21ኛ፤ በ1993 እኤአ በ4ኛው በ1 የወርቅ፣ በ1 የብርና በ1 የነሐስ ሜዳልያ ከዓለም 12ኛ፤ በ1995 እኤአ በ5ኛው ጉተንበርግ ስዊድን ላይ በ1 የወርቅ እና በ1 የብር ሜዳልያ ከዓለም 16ኛ፤ በ1997 እኤአ በ6ኛው አቴንስ ግሪክ ላይ በ1 የወርቅ ሜዳልያ ከዓለም 22ኛ፤ በ1999 እኤአ በ7ኛው ሲቪያ ስፔን ላይ በ2 የወርቅና 3 የነሐስ ሜዳልያ ከዓለም 9ኛ፤ በ2001 እኤአ በ8ኛው ኤድመንትን ካናዳ ላይ በ2 የወርቅ፣ 3 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያ ከዓለም 7ኛ፤ በ2003 እኤአ በ9ኛው ሴንትዴኒስ ፈረንሳይ ላይ በ3 የወርቅ፣ 2 የብርና 2 የነሐስ ሜዳልያ ከዓለም 4ኛ፤ በ2005 እኤአ በ10ኛው ሄልሲንኪ ፊንላንድ ላይ በ3 የወርቅ፣ 4የብርና 2 የነሐስ ሜዳልያ ከዓለም 3ኛ፤ በ2007 እኤአ በ11ኛው ኦሳካ ጃፓን ላይ በ3 የወርቅና 1 የነሐስ ሜዳልያ ከዓለም 4ኛ፤ በ2009 እኤአ በ12ኛው በርሊን ጀርመን ላይ በ2 የወርቅ፣ 2 የብርና 4 የነሐስ ሜዳልያ ከዓለም 7ኛ እንዲሁም በ20011 እኤአ በ13ኛው ዴጉ ደቡብ ኮርያ ላይ በ1 የወርቅና 4 የነሐስ ሜዳልያ ከዓለም 9ኛ ደረጃ ያገኘችበትን ውጤት አስመዝግባለች፡፡ በ2013 እኤአ ላይ በሞስኮው 14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና 3 የወርቅ፤ 4 የብር እና 4 የነሐስ ሜዳልያዎች በመስበሰብ ከዓለም 6ኛ ደረጃ ነበራት፡፡    

Monday, 24 August 2015 10:20

የምንግዜም ውጤት በነጥብ

የእንግሊዙ አትሌቲክስ ዊክሊ ባለፉት 40 ዓመታት የተደረጉትን 14 የዓለም ሻምፒዮናዎች የውጤት ታሪክ በመዳሰስ ባጠናከረው ዝርዝር ዘገባ መሰረት አሜሪካ ፤ ጃማይካ፤ ራሽያ፤ ኬንያ፤ ጀርመን እና ኢትዮጵያ  እንዲሁም ፈረንሳይ፤ቻይና እና እንግሊዝ በተለይ በአትሌቲክስ ውድድድሮች ውጤታማነት ከፍተኛውን ነጥብ በማስመዘገብ እስከ 10 ባለው ደረጃ ይቀመጣሉ፡፡
የአትሌቲስ ዊክሊ ባለፉት 14 የዓለም ሻምፒዮናዎች ከ1 እሰከ 5 የውጤት ደረጃ እና ነጥብ
በሴቶች 800 ሜትር
ራሽያ 81 ነጥብ፤ ጃማይካ 49 ፤ አሜሪካ 39፤ ኩባ 36፤ ኬንያ 34
በሴቶች 3ሺ እና 5ሺ ሜትር
ኢትዮጵያ 113 ነጥብ፤ ኬንያ 96፤ ራሽያ 39፤ ሮማኒያ 33 ፤ ቻይና 33
በሴቶች 10 ሺ ሜትር
ኢትዮጵያ 131 ነጥብ ፤ ኬንያ 92፤ ቻይና 50፤ እንግሊዝ 32፤ አሜሪካ 27
በሴቶች ማራቶን
ጃፓን 118 ነጥብ፤ ኬንያ 62፤ ፖርቱጋል 42፤ ሮማኒያ 37፤ ቻይና 37
በወንዶች 800 ሜትር
ኬንያ 108 ነጥብ፤ አሜሪካ 46፤ ደቡብ አፍሪካ 33፤ ሩስያ 31 ፤ ዴንማርክ 30
በወንዶች 1500 ሜትር
ኬንያ 96 ነጥብ፤ ስፔን 75 ፤ ሞሮኮ 71 ፤ አሜሪካ 46፤ አልጄርያ 37
በወንዶች 5ሺ ሜትር
ኬንያ 144 ነጥብ፤ ኢትዮጵያ  101፤ ሞሮኮ 74፤ አሜሪካ 41፤ ታላቋ ብሪታኒያ 29
በወንዶች 10 ሺ ሜትር
ኢትዮጵያ 165 ነጥብ፤ ኬንያ 146፤ ጀርመን 27፤ ሞሮኮ 26፤ ታላቋ ብሪታኒያ 25
በወንዶች ማራቶን
ኬንያ 70 ነጥብ ፤ጃፓን 65፤ ኢትዮጵያ 58፤ ስፔን 51፤ ጣሊያን 48

Page 4 of 19