ብራዚል ካዘጋጀችው 20ኛው ዓለም ዋንጫ 1 ወር ካለፈ በኋላ የዓለም ስፖርት አፍቃሪ ትኩረት ወደ አምስቱ የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች ዞሮ ቆይቷል፡፡ አምስቱ የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ፤ የስፔን ፕሪሚዬራ ሊጋ፤ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ፤ የጣሊያን ሴሪኤና የፈረንሳይ ሊግ 1 ሲሆኑ በሚቀጥሉት 9 ወራት በከፍተኛ ደረጃ ፉክክር ይደረግባቸዋል፡፡ ከሊጎቹ ከተከፈተ አንድ ሳምንት ያለፈው የፈረንሳይ ሊግ 1 ነው፡፡ ዛሬ እና ነገ  የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ሲጀመር፤ በሚቀጥለው ሳምንት  የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋና የጀርመኑ ቦንደስ ሊጋ እንዲሁም የጣሊያን ሴሪ ኤ ከሁለት ሳምንት በኋላ ይከፈታሉ፡፡
ዩሮ ቶፕ ፉት የተባለ የእግር ኳስ ድረገፅ በሊግና በአህጉራዊ ሻምፒዮናዎች  ያለውን የፉክክር ደረጃና ውጤት በማስላት  ለሊጎቹ ባወጣው ደረጃ የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ በ5887 ነጥብ አንደኛ መሆኑን አመልክቷል፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በ5298 ነጥብ፤ የጣሊያኑ ሴሪ ኤ በ3428 ነጥብ እንዲሁም የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ3348 ነጥብ እስከ 4ኛ ደረጃ ተከታትለው ሲወስዱ፤ የፈረንሳዩ ሊግ 1 በ1877 ነጥብ አምስተኛነቱን 2520 ነጥብ ባስመዘገበው የፖርቱጋሉ ሊግ ተነጥቆ 6ኛ ነው፡፡
በሌላ በኩል ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ አሃዛዊ እና ታሪካዊ መረጃዎች አሰባሳቢ ተቋም የሆነው አይኤፍኤችኤችኤስ በ2014 የዓለም ምርጥ የእግር ኳስ ሊጎች  ደረጃ ባወጣበት ወቅት በ1155 ነጥብ አንደኛ የሆነው የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ ነው፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በ1128 ነጥብ፤ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ1056 ነጥብ እንዲሁም የጣሊያኑ ሴሪ ኤ በ927 ነጥብ እስከ 4ኛ ደረጃ ተከታትለው ሲወስዱ፤ የፈረንሳዩ ሊግ 1 በ796 ነጥብ በብራዚል እና በአርጀንቲና የሊግ ውድድሮች ተበልጦ 7ኛ ነው፡፡ ከዓለም ዋንጫ በኋላ የአውሮፓ ክለቦች   ለአዲሱ የ2014 — 15 የውድድር ዘመን በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ቅድመ ዝግጅት በማድረግ ሰንብተዋል፡፡ ላለፉት 6 ሳምንታት ደግሞ በክረምቱ የተጨዋቾች ዝውውር ገበያ ተሯሩጠዋል፡፡  በውድድር ዘመኑ  ተጠናክረው ለመቅረብ በተለይ በአምስቱ ትልልቅ የአውሮፓ ሊጎች የሚገኙ 25 ክለቦች በገበያው ንቁ ተሳትፎ ነበራቸው፡፡ በ2014 15 የውድድር ዘመን የስፔን ላሊጋ ባርሴሎና ሪያል ማድሪድ ባሰባሰቧቸው ምርጥ ተጨዋቾች ትኩረት ቢያገኝም ከአምስት በላይ የእንግሊዝ ክለቦች በዝውውር ገበያው በርካታ ምርጥ ተጨዋቾችን በማስፈረም መጠናከራቸው ለፕሪሚዬር ሊጉ ሻምፒዮናነት ከባድ ፉክክር እንዲጠበቅ ምክንያት ሆኗል፡፡ ሁለቱ ሊጎች በክረምቱ የዝውውር መስኮት የነበራቸው ወጭ የገበያውን 63 በመቶውን የሸፈነ ነው፡፡ በአንፃሩ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ እና የጣሊያን ሴሪኤ ክለቦች ወጭያቸው በግማሽ ያነሰ ነበር፡፡
ከአውሮፓ ሊጎች ሁለቱ የስፔን ክለቦች ባርሴሎና እና ሪያል ማድሪድ 190.2 ሚሊዮን ዶላር እና 146.3 ሚሊዮን ዶላር ከፍተኛውን ወጭ ያስመዘገቡ ናቸው፡፡ ቼልሲ 124.36  ፤ማን ዩናይትድ 97.62 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም የፈረንሳዩ ፒኤስጂ እና የስፔኑ አትሌቲኮ ማድሪድ እያንዳንዳቸው 78.20 ሚሊዮን ዶላር በላይ  ወጭ  እስከ አምስት ያለውን ተከታታይ ደረጃ አግኝተዋል፡፡በዝውውር ገበያው ውድ ሂሳብ የወጣው በባርሴሎና ሲሆን አወዛጋቢውን የኡራጋይ ተጨዋች ሊውስ ስዋሬዝ በ89.3 ሚሊዮን ዶላር ከሊቨርፑል ላይ የገዛበት ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ከፍተኛው ሂሳብ የተከፈለው በሪያል ማድሪድ ሲሆን ኮሎምቢያዊውን ጄምስ ሮድሪጌዝ ከፈረንሳዩ ክለብ ሞናኮ ለማስፈረም 88.2 ሚሊዮን ዶላር አውጥቷል፡፡ ቼልሲ ብራዚላዊውን ዴቭድ ሊውስ ለፈረንሳዩ ክለብ ፓሪስ ሴንትዠርመን የሸጠበት 54.57 ሚሊዮን ዶላር ሂሳብ ፤ አሁንም ቼልሲ ስፔናዊውን ዲያጎ ኮስታ ከአትሌቲኮ ማድሪድ በ41.9 ሚሊዮን ዶላር የገዛበት እንዲሁም አርሰናል ቺሊያዊውን አጥቂ አሌክሲ ሳንቼዝ ከባርሴሎና ለማዛወር የከፈለው 41.67 ሚሊዮን ዶላር ተከታታይ ደረጃ ይወስዳሉ፡፡
የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ዛሬ ሲጀመር  ሌስተር ሲቲ፤ በርንሌይ እና ኪውንስ ፓርክ ሬንጀርስ ሊጉን የተቀላቀሉ አዲስ ክለቦች ናቸው፡፡ በውድድር ዘመኑ ከሚጠበቁ ፍጥጫዎች ዋንኛው በአዲሱ የማንችስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ሊውስ ቫንጋል እና በቼልሲው ጆሴ ሞውሪንሆ መካከል ለሻምፒዮናነት የሚደረገው እሰጥ አገባ የሞላበት ፉክክር ነው፡፡ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግን ጨምሮ በተለያዩ ሊጎች አራት ክለቦችን ለሊግ ሻምፒዮናነት ያበቁት ሆላንዳዊው ሊውስ ቫንጋል  የማንችስተር ዩናይትድን የሃያልነት ክብር ለመመለስ ተስፋ ተጥሎባቸዋል፡፡
በዛሬዎቹ የመክፈቻ ጨዋታዎች ለዋንጫ ከሚፎካከሩት አምስቱ ክለቦች መካከል የሚጫወቱት ከሜዳው ውጭ ኪውፒአርን የሚገጥመው ቼልሲ እና በኦልድትራፎርድ ስዋንሴን የሚያስተናግደው ማንዩናይትድ ይሆናሉ፡፡ ሌሎቹ ትልልቅ ክለቦች በነገው እለት የመክፈቻ ግጥሚያቸውን ያደርጋሉ፡፡ ያለፈው ዓመት የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ማንቸስተር ሲቲ የውድድር ዘመኑን የሚከፍተው ከሜዳው ውጭ ከኒውካስትል ዩናይትድ ጋር በሚያደርገው ፍልሚያ ነው፡፡ በሌላ በኩል ባለፈው የውድድር ዘመን የኤፍ ኤካፕ ዋንጫን ያነሳውና ከሳምንት በፊት የሊግ ካፕ ዋንጫን ማንቸስተር ሲቲን በመርታት የውድድር ዘመኑን በዋንጫ ድል የከፈተው አርሰናል በሜዳው ከክሪስታል ፓላስ ጋር ይጫወታል፡፡ በሌላ በኩል በታሪኩ ለ84ኛ ጊዜ በሚደረገው የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ ከሚሳተፉ 20 ክለቦች ሰባቱ አዳዲስ አሰልጣኞች በመያዝ በውድድሩ ሲገቡ ባርሴሎና፤ ዲፖርቲቮ ላካሩኛ እና ሴልታ ቪጎ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ላሊጋው ከመጀመሩ አንድ ወር ቀደም ብሎ ማነጋገር የጀመረው ሊውስ ስዋሬዝ በባርሴሎና ክለብ የሚኖረው ሚና ነው፡፡ በክለቡ ባርሴሎና ከኔይማር እና ከሜሲ ጋር የሚጫወትበት አሰላለፍ እና ፉክክር ማነጋገሩን ቀጥሏል፡፡ ስዋሬዝ ንክሻውን ስላለመድገሙ በተነሱ ክርክሮችም ሰፊ ሽፋን ሲያገኝ ሰንብቷል፡፡

ባለፉት 10 ዓመታት በዓለም እግር ኳስ የቢሊዬነሮች ሚና እና የኢንቨስትመንት ድርሻ እያደገ መጥቷል፡፡ በተለይ በአውሮፓ አምስት ታላላቅ ሊጎች   በቢሊዬነሮች ሙሉ ለሙሉ በባለቤትነት በመያዛቸውና በከፍተኛ የአክሲዮን ድርሻ ኢንቨስት ስለተደረገባቸው  የፉክክር ደረጃቸውን ያሳደጉ ከ10 በላይ ክለቦች ናቸው፡፡ በአንፃሩ  የቢሊዬነሮች ኢንቨስትመንት ያለደረሰላቸው በርካታ የአውሮፓ  ክለቦች ምንም እንኳን በየሊጎቹ በቴሌቭዥን ስርጭት መብት እና በተያያዥ ንግዶች  ገቢያቸው ቢጠናከርም በዋንጫ ተፎካካሪነታቸው ያን ያህል እየተሳካላቸው አይደለም፡፡  በክለቦች ደረጃ በሚደረጉ የውስጥ ውድድሮች እና አህጉራዊ ሻምፒዮናዎች ላይ በሚገኝ ስኬት ቢሊዬነሮች ተማርከዋል፡፡ ወደ እግር ኳሱ የመሳባቸው ዋና ምክንያት ትርፋማነቱ  እንደሆነም ይገለፃል፡፡
ታዋቂው የቢዝነስ መፅሄት ፎርብስ በሰራው ጥናት  መሰረት በመላው ዓለም በእግር ኳስ ክለብ  ሙሉ ባለቤትነት እና የአክሲዮን ድርሻ ያላቸው ቢሊዬነሮች ከ50 በላይ ሆነዋል፡፡ እነዚህ ቢሊዬነሮች በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች የተሳካላቸው ሲሆኑ አሜሪካውያን ነጋዴዎች፤ ኤስያውያን  ቱጃሮች፤ የአረቡ ዓለም ንጉሳውያን ቤተሰብ አባላት፤ የራሽያ ቢሊየነሮች ዋና ዋናዎቹ  ናቸው፡፡ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ተወዳዳሪ ከሆኑ 20 ክለቦች መካከል 7 ያህሉ ከሌላ አገር በመጡ ቢሊዬነር ኢንቨስተሮች የተያዙ ናቸው፡፡  ባለፉት ሶስት እና አራት ዓመታት የቢሊዬነሮችን ትኩረት በመሳብ የስፔንና የፈረንሳይ ክለቦችም እየቀናቸው ናቸው፡፡
የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች በአፍሪካ፤በኤስያ በዓረቡ ዓለም እና በሰሜን አሜሪካ በሚያገኙት ትኩረት ቢሊዬነሮቹ  ይማረካሉ። ከፍተኛ ኢንቨስትመንት በመላው ዓለም ለሚያንቀሳቅሱባቸው ኩባንያዎች የክለቦቹ ስኬት አስደናቂ የገፅታ ግንባታ ያስገኝላቸዋል። የእግር ኳስ ክለቦች እንደ አሰተማማኝ  ንብረት መታየታቸው ሌላው ጉልህ ጠቀሜታ ነው፡፡ በዓለም እግር ኳስ ክለቦች  አጠቃላይ የዋጋ ግምት በተሰራው ደረጃ  የስፔኑ ክለብ ሪያል ማድሪድ በ3.4 ቢሊዮን ዶላር ዋጋው በመተመን አንደኛ ደረጃ  ሲይዝ ባርሴሎና በ3.2 ቢሊዮን ዶላር ይከተለዋል፡፡  ማንችስተር ዩናይትድ በ3.17 ቢሊዮን ዶላር ሶስተኛ ደረጃ ሲያገኝ፤ ባየር ሙኒክ በ1.85 ቢሊዮን ዶላር፤ አርሰናል በ1.33 ቢሊዮን ዶላር፤ ቼልሲ በ901 ሚሊዮን ዶላር፤ ማንችስተር ሲቲ በ689 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም ሊቨርፑል በ651 ሚሊዮን ዶላር አጠቃላይ የዋጋ ተመናቸው ተከታታይ ደረጃ አላቸው፡፡ እንደ ፎርብስ መፅሄት ጥናት በአጠቃላይ የዋጋ ግምታቸው እስከ 20 ደረጃ የተሰጣቸው የእግር ኳስ ክለቦች አማካይ ተመን  968 ሚሊዮን ዶላር ሲሆን ይህም ካለፈው የውድድር ዘመን በ26 በመቶ እድገት ማሳየቱን ጠቁሟል፡፡
በእግር ኳስ ስፖርት እየተጠናከረ የመጣው የቢሊዬነሮች ኢንቨስትመንት  በየሊጎቹ ለዋንጫ የሚፎካከሩ ክለቦችን አብዝቷል፡፡ የክለቦችን የተጨዋች ስብስብ በማጠናከር እና የዝውውር እና የደሞዝ ክፍያቸውን በማሳደግ ተጠቃሚ እያደረጋቸው ነው፡፡ የቢሊዬነሮቹ ኢንቨስትመንት  ጎን ለጎን አሉታዊ ተፅኖዎችን ማሳደሩም አልቀረም፡፡ በአውሮፓ አምስት ታላላቅ ሊጎች በቢሊዬነሮቹ በጀት የሚንቀሳቅሱ  ክለቦች ውስጥ ያሉ ተጨዋቾች፤ አሰልጣኞች እና ሌሎች ባለሙያዎች በየክለቦቻቸው ለረጅም ጊዜ በታማኝነት የሚያገለግሉበትን ሁኔታ ሲያቀዘቅዝባቸው፤ ደጋፊዎች በክለቦቻቸው ያላቸውን ሚናም በከፍተኛ ደረጃ እየቀነሰ መሆኑ  ይተቻል፡፡  
አብራሞቪችና ሌሎች የሩስያ ቱጃሮች
በእግር ኳስ ክለብ ባለቤትነት  በጣም ስኬታማ የሚባሉትና በፈርቀዳጅነት የሚጠቀሱት ራሽያዊው ሮማን አብራሞቪች ናቸው። የነዳጅ ኩባንያ ባለቤት የሆኑት አብራሞቪች በቼልሲ ክለብ ባለቤትነት 12 ዓመታት አስቆጥረዋል፡፡  በመጀመርያዎቹ 3 እና አራት አመታት ብዙም ባይሳካላቸውም ካለፉት 5 ዓመታት ወዲህ ግን የላቁ ክብሮችን  በማግኘት  ተክሰዋል፡፡
አብራሞቪች ቼልሲን  በባለቤትነት ከያዙት በኋላ የተገኙ ስኬቶች ገንዘብ ያመጣቸው እንጅ በተመጣጣኝ የፉክክር ደረጃ የተገኙ አይደለም በሚል በተደጋጋሚ ትችት ቀርቧል፡፡ የምዕራብ ለንደኑ ክለብ ቼልሲ 3 የፕሪሚዬር ሊግ፤ አራት የኤፍኤ ካፕ፤ 2 የሊግ ካፕ እና በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒዮን በመሆን የሻምፒዮንስ ሊግ እና የዩሮፓ ሊግ የዋንጫ ክብሮችን  አግኝቷል፡፡  አብራሞቪች ክለቡን ከያዙት ግዜ ጀምሮ ከ1.3 ቢሊዮን ዶላር በላይ ወጭ አድርገውበታል፡፡ በየዝውውር መስኮቱ ወቅት በአማካይ 50 ሚሊዮን ዶላር በማውጣት ምርጥ ተጨዋች የሚገዛ ክለብ ሆኗል። አብራሞቪች ቼልሲን የገዙት በ334 ሚሊዮን ዶላር ነበር፡፡ አሁን ሊሸጡት ቢፈልጉ ክለቡ ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ያወጣል፡፡
ከአብራሞቪች በኋላ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ብቻ ሳይሆን በሌሎች የአውሮፓ ትልልቅ ሊጎች እና በአገራቸው ባሉ ክለቦችም ከ5 በላይ የራሽያ ቢሊዬነሮች  ኢንቨስት አድርገዋል፡፡ አንደኛው ቢሊዬነር በአርሰናል ክለብ ድርሻ ያላቸውና ክለቡ የሚመካበትን የኤምሬትስ ስታድዬም እንዲገነባ ከፍተኛ ድርሻ የነበራቸው አሊሸር ኡስማኖቭ ናቸው፡፡ ሌላኛው ደግሞ የፈረንሳይ ክለብ የሆነውን ሞናኮን በባለቤትነት የያዙት ዲምትሪ ራይቦሎቬሌቭ ናቸው፡፡ ሌሎቹ የራሽያ ቢሊዬነሮች በአገሮቻቸው ባሉ ክለቦችም አስደናቂ ኢንቨስትመንት አድርገዋል፡፡ የእንግሊዙ ክለብ ቼልሲ ባለቤት አብራሞቪች በራሽያ ያለውን ዜንት ፒትስበርግ በመደገፍ ሲሰሩ ቆይተዋል፡፡ በ2011 እኤአ  ከተመሰረተ 20 ዓመት የሚሆነው ወጣት ክለብ አንዚ ማክቻሃቻካላ ሌላ   ቢሊዬነር በመግዛት ወደ አህጉራዊ ውድድር አሳድገውታል፡፡
ሼክ መንሱንና የዓረቡ ዓለም ኢንቨስትመንት
የመካከለኛው ምስራቅ በተለይ በኳታር እና በዱባይ ያሉ የንጉሳውያን ቤተሰብ አባላት ካለፉት አምስት አመታት ወዲህ በአውሮፓ እግር ኳስ በስፋት ተሰማርተዋል፡፡ እነዚህ የአረቡ አለም ቢሊዬነሮች ክለቦችን በባለቤትነት በመያዝ ብቻ ሳይሆን በትልልቅ ኩባንያዎቻቸው የማልያ፤ የስታድዬም ግንባታ የስፖንሰርሺፕ ድጋፎችን በስፋት በመስጠት ጥቂት የማይባሉ ክለቦችን አጠናክረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በአውሮፓ እግር ኳስ የመካከለኛው ምስራቅ አየር መንገዶች ከ20 የአውሮፓ ትልልቅ ክለቦች በሰባቱ ስፖንሰርሺፕ ሰጥተዋል፡፡ ኳታር ኤርላይንስ በባርሴሎና፤ ፍላይ ኤምሬትስ በሪያል ማድሪድ፤ በፒኤስጂ፤ በአርሰናል እና በኤሲ ሚላን፤ ኢትሃድ ኤርዌይስ በማንችስተር ሲቲ የማልያ ስፖንሰሮች  ናቸው። ከዓረቡ ዓለም የእግር ኳስ ኢንቨስትመንት አድራጊ ቢሊዬነሮች ግዙፍ ለውጥ የታየው በእንግሊዙ ክለብ ማንችስተር ሲቲ ነው። ማንችስተር ሲቲ የአቡዳቢ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ባለቤቶች በሆኑት የኳታር ንጉሳዊ ቤተሰብ ከ6 ዓመት በፊት ተይዟል፡፡ የአቡዳቢ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ያለው ሃብት እስከ  22 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ነው፡፡ የሚያስተዳድሩት ሼክ መንሱን ቢን ዛይድ  ሲቲን የገዙት በ321 ሚሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንታቸውም ነበር። ባለፉት 5 ዓመታት ክለቡን ለማጠናከር ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ፈሰስ አድርገዋል፡፡  ማንችስተር ሲቲ በአቡዳቢ ኢንቨስትመንት ግሩፕ መደገፍ ከጀመረ ወዲህ ከ44 ዓመት በኋላ የመጀመርያውን የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮናነት ማግኘቱ እና ከዚያም ሁለተኛውን መድገሙ ይታወቃል፡፡ ባለፉት ሶስት አመታት ክለቡ በእንግሊዝ እና በአውሮፓ ደረጃ የላቀ ውጤት እና ተፎካካሪነት እንዲኖረው ማድረግ ተችሏል፡፡
በ2011 እኤአ ላይ ታዋቂውን ፓሪስ ሴንትዠርመን ባበለቤትነት የያዘው የኳታር ኢንቨስትመንት አውቶሪቲ ነው፡፡ ይህ ባለቤትነት ፒኤስጂን የፈረንሳይ አንደኛ ሃብታም ክለብ አድርጎታል፡፡ ክለቡ ከ20   ዓመታት በኋላ የሊግ ሻምዮን ለመሆን በቅቷል፡፡ ባለቤቶቹ ክለቡን ለማጠናከር በተጨዋቾች ግዢ ብቻ ከ300 ሚሊዮን ዶላር በላይ አውጥቷል፡፡
በፕሪሚዬር ሊግ የተማረኩት አሜሪካውያና ኤስያውያን
ቢያንስ በስድስት የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች ላይ በባለቤት እና በአክሲዮን ድርሻ ያላቸው አሜሪካውያን ቢሊዬነሮች ናቸው፡፡ ሌርነር በአስቶንቪላ፤ የግሌዘር ቤተሰብ በማንችስተር ዩናይትድ፤ ስታን ክሮንኬ በአርሰናል፤ ኢሊስ ኾርት በሰንደር ላንድ ጆርጅ ኤሊት እና ቶም ሂክስ በሊቨርፑል ኢንቨስት ያደረጉ አሜሪካውያን ናቸው፡፡ የፉልሃምና የሰንደርላንድ ክለቦች ላይ ኢንቨስት ያደረጉ ሌሎች ሁለት  ቢሊዬነሮችም አሉ፡፡ አሜሪካውያኑ ከቤዝቦል እና ፉትቦል ክለቦች ባለቤትነት ወደ አትራፊው ፕሪሚዬር ሊግ ኢንቨስት የማድረግ ፍላጎታቸው አድጓል፡፡ በዋናነት በቲቪ ስርጭት ሊጉ በመላው ዓለም የሚያገኘው ሽፋን እና ተወዳጅነት በመማረካቸው ነው፡፡ ኤስያውያንም በአውሮፓ እግር ኳስ ኢንቨስትመንት ንቁ ተሳትፎ ማድረግ ከጀመሩ ቆይተዋል፡፡ በተለይ በደቡብ ኤስያ ባሉ አገራት ያሉ ቢሊዬነሮች በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ኢንቨስት እያደረጉ ናቸው፡፡  ኪውፒ አር፤ካርዲፍሲቲ፤ ሌስተርሲቲ በኤስያውያን ቢሊዬነሮች ባለቤትነት ተይዘዋል፡፡ ሲንጋፖራዊው ቢሊዬነር ፒተር ሊም የስፔኑን ክለብ ቫሌንሽያ በባለቤትነት የተቆጣጠሩት ባለፈው አመት ነው፡፡ ቢሊዬነሩ ቫሌንሽያን ሲረከቡ የራሳቸው እግር ኳስ ክለብ በባለቤትነት ለማስተዳደር የረጅም ግዜ ህልሜን አሳክቻለሁ ብለዋል፡፡
ክለቦች  ያሏቸው ቢሊዬነሮችና የሃብታቸው ደረጃ
በዓለም ታዋቂ የእግር ኳስ ክለብ ባለቤቶችና አክሲዮን ድርሻ ያላቸውን ባለሃብቶች ያላቸውን የሃብት ግምት በማስላት እስከ 20ኛ ደረጃ ያወጣላቸው “ዌልዝ ኤክስ” የተባለ የመረጃ ተቋም  ነው፡፡ እንደ ዌልዝ ኤክስ መረጃ  በተለይ በአውሮፓ ታላላቅ ሊጐችና በአሜሪካ ሜጀር ሶከር  ሊግ በሚወዳደሩ ክለቦች ሙሉ  ባለቤትነትና ከፍተኛ አክሲዮን ድርሻ  ያላቸው ቢሊዬነሮች ሃብት የተመዘገበላቸው ከፍተኛው 73 ዝቅተኛው 5 ቢሊዮን ዶላር ነው፡፡ በአጠቃላይ የሃብታቸው ግምት ወደ 290 ቢሊዮን ዶላር ይጠጋል፡፡ ዌልዝ ኤክስ በክለብ ባለቤት ቢሊዬነሮች ላይ በሰራው ደረጃ መሰረት እስከ 20ኛ  11 የተለያዩ አገራት ዜጋ ቢሊዬነሮች ተካትተዋል፡፡ በአጠቃላይ የሃብታቸው ግምት ወደ 290 ቢሊዮን ዶላር ይጠጋል፡፡ ከ1 እስከ አምስት ደረጃ የሚሰጣቸው ቢሊዬነሮች የክለብ ባለቤቶች  የሚከተሉት ናቸው፡፡ ዌልዝ ኤክስ በሃብት ግምት እና መረጃ የታወቀ ተቀማጭነቱን በሲንጋፖር ያደረገና በአምስቱም አህጉራት የሚንቀሳቀሰ ተቋም ነው፡፡
1.ካርሎስ ስሊም
የሃብት ግምት — 73 ቢሊዮን ዶላር
በሶስት ክለቦች የአክሲዮን ድርሻ አላቸው ሁለቱ ፓችዋ እና ሌዎን የተባሉ የሜክሲኮ ክለቦች ሲሆኑ አንደኛው ደግሞ የስፔኑ ክለብ ሪያል ኦቪዬዶ ነው፡፡
ሜክሲኳዊ የቴሎኮም ኢንቨስተር ካርሎስ ስሊም 74 ዓመታቸው ሲሆን ከ2010 እኤአ ጀምሮ የዓለም ሃብታሞችን ደረጃ በየዓመቱ በአንደኝነት እየመሩ ናቸው፡፡ ግሩፖ ካርሶ በተባለ ግዙፍ ኩባንያቸው በቴሌኮም፤ በሪል ስቴት፤ በአየር መንገድ፤ በሚድያ፤ ቤክኖሎጂ እና በፋይናንስ ኢንቨስትመንታቸው በበርካታ የሜክሲኮ ኩባንያዎች ከፍተኛ ድርሻ አላቸው፡፡ በተለይ በ49 ቢሊዮን ዶላር ካፒታል የሚንቀሳቀሰው አሜሪካ ሞቪል የላቲን አሜሪካ ግዙፉ የቴልኮም ኩባንያ ነው፡፡
2.አማንስዮ ኦርቴጋ
የሃብት ግምት 65.6 ቢሊዮን ዶላር
ክለብ ዲፖርቲቮ ላካሩኛ
ኢንድቴክስ ግሩፕ የተባለ ግዙፍ ዓለም አቀፍ ኩባንያን በፕሬዝዳንትነት የሚያስተዳድሩት የ78 ዓመቱ አማንስዮ ኦርቴጋ በስፔን እና በዓለም አቀፍ የፋሽን ኢንዱስትሪ ከፍተኛ ዝና ያላቸው በሃብታቸው ግምት በዓለም ሶስተኛ ዴጃ ላይ ይገኛሉ፡፡ አመንስዮ ኦርቴጋ በዲፖርቲቮ ላካሩኛ ክለብ ባለቤትነት ለየት የሚያደርጋቸው እያንዳንዱን የክለቡ ጨዋታ ከክለቡ ቀንደኛ ደጋፊዎች ጋር በመመልከት ዝነኛ መሆናቸው ነው፡፡
3. አሊሸር ኡስማኖቭ
የሃብት ግምት 18.6
ክለብ አርሰናል
ራሽያዊው  በማእድን ቁፈራ እና በብረታብረት ኢንዱስትሪ በሚንቀሳቀስ ኩባንያቸው የናጠጡ ሃብታም ለመሆን የበቁ ናቸው። አሊሸር ኡስማኖቭ በታዋቂው ሲልከን ቫሊ ከፍተኛ የአክሲዮን ድርሻ አላቸው፡፡ ኡስማኖቭ በ2007 እኤአ ላይ በሰሜን ለነድኑ ክለብ አርሰናል 17 በመቶ ድርሻ በመግዛት ክለቡን ሲደግፉት ቆይተዋል፡፡
4.ጆርጅ ሶሮስ
የሃብት ግምት 19.6 ቢሊዮን ዶላር
ክለብ ማንችስተር ዩናይትድ
አሜሪካዊ ነጋዴ ጆርጅ ሶሮስ በማንችስተር ዩናይትድ ክለብ 7.85 በመቶ ከፍተኛው የአክሲዮን ድርሻ አላቸው፡፡ በኦልድትራፎርዱ ክለብ ኢንቨስት ያደረጉት ሶሮስ ፈንድ ማኔጅመንት በተባለ ኩባንያቸው ነው፡፡
5. ፖል አለን
የሃብት ግምት 15 ቢሊዮን ዶላር
ክለብ ሲያትል ሳውንድረስ  
አሜሪካዊ ነጋዴ ፖል አለን ታላቁን የማይክሮሶፍት ኩባንያ ከመሰረቱ ባለሃብቶች ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ናቸው፡፡
ህንዳዊው ላክሺም ሚታል በ15 ቢሊዮን ዶላር በኪውንስ ፓርክ ሬንጀርስ፤ ሪህና አኬሜቶቭ በ15 ቢሊዮን ዶላር በዩክሬን ሊግ በሚወዳደረው ሻካታር ዶንቴስክ፤ ፈረንሳዊው ፍራንኮይስ ሄነሪ ፒናልት በ14 ቢሊዮን ዶላር በሊግ 1 በሚወዳደረው ስታድ ዲ ሬኔስ፣ ራሽያዊው ሮማን አብራሞቪች በ12 ቢሊዮን ዶላር በቼልሲ እንዲሁም ጆን ፍሬድክሰን በ12 ቢሊዮን ዶላር በኖርዌይ ሊግ በሚወዳደረው ቫሌሬንጋ  ክለብ እስከ 10 ያለውን ደረጃ ወስደዋል፡፡  እስከ 20ኛ ባለው ደረጃ የሞናኮ ክለብ ባለቤት ራሽያዊው ዲምትሪ ራይቦሎቬሌቭ በ10 ቢሊዮን ዶላር ፤ የኤሲሚላን  ክለብ ባለቤት ሲልቭዮ በርልስኮኒ በ7 ቢሊዮን ዶላር እንዲሁም የማንችስተር ሲቲው ሼክ መንሱር ቢንዘየድ በ7 ቢሊዮን ዶላር ከ12 እስከ 15ኛ ደረጃ ሲሰጣቸው፤ በአርሰናል ክለብ 38 በመቶ ድርሻ ያላቸው አሜሪካዊ ቢሊዬነር ስታን ክሮንኬ በ4 ቢሊዮን ዶላር 19ኛ ደረጃ አላቸው፡፡


20 ክለቦች ፤ 5.3 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጡ 516 ተጨዋቾች   
በተጨዋች ስብስብ ውዱ ክለብ — ማን ሲቲ 647.7 ሚሊዮን ዶላር
ውዱ ተጨዋች —  የማንችስተር ሲቲው ኤዲን ሃዛርድ በ63.84 ሚሊዮን ዶላር
በ84ኛው የስፔን  ፕሪሚዬራ ሊጋ
20 ክለቦች 4.01 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጡ 491 ተጨዋቾች
በተጨዋች ስብስብ ውዱ ክለብ —ሪያል ማድሪድ 953.61 ሚሊዮን ዶላር
ውዱ ተጨዋች — የባርሴሎናው ሊዮኔል ሜሲ በ159.6 ሚሊዮን ዶላር
በ52ኛው የጀርመን ቦንደስ ሊጋ
18 ክለቦች 3.64 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጡ 518 ተጨዋቾች
በተጨዋች ስብስብ ውዱ ክለብ — ባየር ሙኒክ 708.23 ሚሊዮን ዶላር
ውዱ ተጨዋች — የባየር ሙኒኩ ሮበርት ሌዎንዳውስኪ በ66.5 ሚሊዮን ዶላር
በ83ኛው የጣሊያን ሴሪ ኤ
20 ክለቦች 3.4 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጡ 516 ተጨዋቾች
በተጨዋች ስብስብ— ውዱ ክለብ ጁቬንትስ 450.4 ሚሊዮን ዶላር
ውዱ ተጨዋች— የጁቬንትሱ አርትሮ ቪዳል በ70 ሚሊዮን ዶላር
በ77ኛው የፈረንሳይ ሊግ 1
20 ክለቦች 2.11 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጡ 540 ተጨዋቾች
በተጨዋች ስብስብ ውዱ ክለብ — ፓሪስ ሴንትዠርመን  513.38 ሚሊዮን ዶላር
ውዱ ተጨዋች —የፓሪስ ሴንትዠርመኑ ኤድሰን ካቫኒ በ79.8 ሚሊዮን ዶላር

በከፍተኛ ድብርትና በመንፈስ ጭንቀት ሲሰቃይ ነበር
ታዋቂው የሆሊውድ የፊልም ተዋናይና ኮሜዲያን አሜሪካዊው ሮቢን ዊሊያምስ በተወለደ በ63 አመቱ ባለፈው ሰኞ ከቀትር በኋላ ከሳን ፍራንሲስኮ በስተሰሜን ቲቡሮን አቅራቢያ በሚገኘው መኖሪያ ቤቱ መኝታ ቤት ውስጥ ራሱን በቀበቶ በማነቅ እንዳጠፋ ቢቢሲ ዘገበ፡፡
‘ጉድሞርኒንግ ቬትናም’ና ‘ዴድ ፖየትስ ሶሳይቲ’ን በመሳሰሉ በርካታ ተወዳጅ ፊልሞቹ የሚታወቀውና የኦስካር ተሸላሚው ተዋናይ ሮቢን ዊሊያምስ፣ ለረጅም ጊዜያት በከፍተኛ ድብርትና በመንፈስ ጭንቀት ይሰቃይ እንደነበርና በቅርቡም ወደ አእምሮ ህክምና መስጫና ማገገሚያ ማዕከል አምርቶ ከዚህ ቀደም አቋርጦት የነበረውን ህክምና መከታተልና እንክብካቤ ማግኘት ጀምሮ እንደነበር ፖሊስን ጠቅሶ ዘገባው አስረድቷል፡፡
ተዋናዩ የአልኮል መጠጥ ሱስ ተጠቂ እንደነበር የጠቆመው ዘገባው፣ ከዚህ ሱስ ለመውጣት የሚያደርገውን ትግል በኮሜዲ ስራዎቹ ውስጥ በግልጽ ይናገር እንደነበር ገልጧል፡፡
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ የተዋናዩን ሞት አስመልክተው ለቤተሰቦቹ በላኩት የሃዘን መግለጫ መልዕክት፣ “ሮቢን ዊሊያምስ ውስጣችንን ኮርኩሮ ሲያስቀን፣ ልባችንን ሰርስሮ ሲያስለቅሰን ኖሮ ያለፈ ልዩ ሰው ነው፡፡ እሱ በሰው አገር ከሚገኙ ወታደሮቻችን፣ በገዛ አገራችን ጎዳናዎች ላይ ተገልለው እስከሚገኙ ዜጎች በሁሉም ልብ ውስጥ አሻራውን ማስቀመጥ የቻለ ድንቅ ሰው ነው” ብለዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ1951 ኤሊኖይስ ውስጥ የተወለደው ሮቢን ዊሊያምስ በተለያዩ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች ላይ ለረጅም አመታት የስታንዳፕ ኮሜዲ ስራዎቹን ሲያቀርብ የቆየ ሲሆን፣ እ.ኤ.አ በ1998 በምርጥ ረዳት ተዋናይነት የኦስካር ተሸላሚ ያደረገውን ‘ጉድ ዊል ሃንቲንግ’ ጨምሮ በበርካታ ተወዳጅ ፊልሞች ላይ በመስራት የትወና ብቃቱን ያስመሰከረ ተዋናይ ነበር፡፡ በርካታ የሆሊውድ ተዋንያንና አለማቀፍ አርቲስቶች የሃዘን መግለጫቸውን እየሰጡለትና ድንቅ የትወና ችሎታውን በተለያዩ የዓለማችን ታዋቂ መገናኛ ብዙሃን እየመሰከሩ የሚገኙለት ሮቢን ዊሊያምስ፣ ከቀድሞ ትዳሩ ያፈራቸው የሶስት ልጆች አባት መሆኑን ዘገባው ገልጧል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

ከ900 በላይ የሚሆኑ የዓለማችን ታዋቂ ደራሲያን ከመጽሃፍት ሽያጭ ጋር በተያያዘ በደል ፈጽመህብናል፤ አንተ በሚሊዮኖች ዶላር እያፈስክ እኛ ግን ማግኘት የሚገባንን ያህል ገንዘብ እያገኘን አይደለም፤  ህልውናችን አደጋ ላይ ወድቋል፤ የምትከተለውን የመጽሃፍት ሽያጭ አሰራር በአፋጣኝ አስተካክል ሲሉ አማዞን ለተሰኘው የድረገጽ ሽያጭ ኩባንያ ማመልከቻ ማስገባታቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ከአለማችን ታላላቅ አሳታሚ ኩባንያዎች አንዱ በሆነው ‘ሃቼቴ’ አማካይነት መጽሃፍቶቻቸውን እያሳተሙ ለንባብ ሲያበቁ የቆዩት እነዚህ ታዋቂ ደራሲያን፣ ከአሳታሚው መጽሃፍቱን እየተረከበ ለገበያ የሚያቀርበው አማዞን እየተከተለው የሚገኘው የሽያጭ ስርዓት ከመጽሃፍቶቻችን ሽያጭ ተገቢውን ገንዘብ እንዳናገኝ የሚያደርግ ነው በማለት ነው አቤቱታቸውን ያቀረቡት፡፡
ደራሲያኑ ለአማዞን በላኩትና በኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣ ላይ ታትሞ ለንባብ በበቃው በዚህ ማመልከቻ እንዳሉት፣ አማዞን መጽሃፍትን በወቅቱ ለደንበኞቹ አለማድረሱ፣ የቅድመ ክፍያ ትዕዛዞችን መቀበል ማቆሙና ጄኪ ሮውሊንግና ስቴፋኒ ሜየርን በመሳሰሉ አንዳንድ የኣለማችን ታዋቂ ደራሲያን መጽሃፍት ላይ የነበረውን ዋጋ ቅናሽ ማቆሙ የሚገባንን ጥቅም እንዳናገኝ አድርጎናል ብለዋል፡፡
አማዞን ከመጽሃፍት ባለፈ ማንኛውንም የሸቀጥ አይነት ለገበያ የሚያቀርብ ከአለማችን ታላላቅ ኩባንያዎች አንዱ የመሆን ህልሙን ለማሳካት በጀመረው ጉዞ ውስጥ የኛ ድርሻ ከፍተኛ ነው ያሉት ደራሲያኑ፣ ኩባንያው የደራሲያኑን ስራዎች ሲሸጥ በቆየባቸው አመታት በሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር ማፍራቱን አስታውሰዋል፡፡
ይሄም ሆኖ ግን አማዞን ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ የጀመረው አዲስ የሽያጭ አሰራር፣ ብዙ ሃብት ያካበተባቸውን ደራሲያን የሚጎዳና ህልውናቸውን አደጋ ላይ የሚጥል በመሆኑ አሰራሩን በአፋጣኝ እንዲያስተካክል ለመጠየቅ መገደዳቸውን በጋራ ባስገቡት ማመልከቻ እንደገለጹ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ሃቼቴ በተባለው አሳታሚ ኩባንያ አማካይነት ስራቸውን ለአንባቢ ከሚያደርሱትና ጉዳዩ በቀጥታ ከሚመለከታቸው ማልኮም ግላድዌል፣ ጄምስ ፓተርሰንና ዶና ታርትን የመሳሰሉ ደራሲያን በተጨማሪም፣ በሌሎች አሳታሚዎች የሚያሳትሙ ጆን ግሪሻምና ሴተፈን ኪንግን የመሳሰሉ ሌሎች የአለማችን ዝነኛ ደራሲያንም የአማዞንን ድርጊት በመቃወም በማመልከቻው ላይ ፊርማቸውን አስቀምጠዋል፡፡  አማዞን ከአሳታሚው ኩባንያ ጋር ባደረገው ስምምነት የደራሲያኑን መጽሃፍት በድረገጽ አማካይነት ሲሸጥ ቢቆይም፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በሽያጩ ላይ ያልተገባ ድርጊት ይፈጸማል በሚል በመካከላቸው አለመስማማት ተፈጥሯል፡፡
አማዞን በቅርቡ ባወጣው መግለጫ በድረገጽ አማካይነት ለሽያጭ የሚበቁ ኤሌክትሮኒክ መጽሃፍት አብዛኞቹ በ9.99 ዶላር መሸጥ ሲገባቸው በ14.99 ዶላር እየተሸጡ እንደሚገኙና ዋጋቸው ያለአግባብ ውድ መሆኑን በመጥቀስ የዋጋ ቅናሽ ማድረግ እንደሚገባ ተናግሮ ነበር፡፡
ዋጋን በመቀነስ ብዙ መጽሃፍትን መሸጥና ከብዛት ትርፍን ማሳደግና ከሚገኘው ትርፍም ለአሳታሚው ኩባንያም ሆነ ለደራሲያኑም የተወሰነ ገንዘብ መስጠት እንደሚቻል በገለጸበት ወቅት፣ ከ 7 ሺህ በላይ ደራሲያን ጉዳዩን በመደገፍ ከአማዞን ጋር ለመስራት መፈራረማቸውንም ዘገባው አስታውሷል።

Published in ከአለም ዙሪያ
Saturday, 16 August 2014 11:09

ሐማስ

          ሰሞኑን በእስራኤልና በፍልስጤም መካከል በተቀሰቀሰውና በተፋፋመው ውጊያ 1ሺ800 ፍልስጤማውያንና 67 አይሁዳውያን ለህልፈት መዳረጋቸው ይታወቃል፡፡ የዚህ አጭር ጽሑፍ አላማ ስለዚህ አስከፊና ጋዛን የድንጋይ ክምር እያደረገ ስላለ ጦርነት ትንተና ለመስጠት አይደለም፡፡ ይልቁንም የእስራኤል ቀንደኛ ጠላት ስለሆነው ሐማስ አንዳንድ ነጥቦችን ለማስጨበጥ ነው፡፡ ሐማስ የአረብኛ ምህፃረ ቃል ሲሆን harkat muqawamah Islamya ወይም ደግሞ በእንግሊዝኛ Islamic resistance movement የሚል ትርጉም ይሰጣል፡፡
ሐማስ የፍልስጤም ሱኒ ኢስላማዊ ድርጅት ሲሆን የተደራጀ ወታደራዊ ክንፍ አለው፡፡ ይህ ወታደራዊ ክንፍ izzad al quassam በመባል ይታወቃል፡፡ ከ2007 ዓ.ም ጀምሮ አብዛኛውን የፍልስጤም ፓርላማ መቀመጫዎችን ካሸነፈ በኋላ ጋዛን ሲያስተዳድር ቆይቷል፡፡
ሀማስ በእስራኤል፣ በአሜሪካ፣ በእንግሊዝ፣ በካናዳ፣ በአውሮፓ ህብረት፣ በግብጽና ዮርዳኖስ በአሸባሪነት የተፈረጀ ድርጅት ሲሆን በአንፃሩ በኢራን፣ በሩሲያ፣ በቱርክ፣ በቻይናና በሌሎች በርካታ አረብ አገራት እንደአሸባሪ ድርጅት አይታይም፡፡ ሐማስ የተመሰረተው ፍልስጤምን ከእስራኤል ይዞታ ነፃ አውጥቶ እስላማዊ መንግስት በዌስት ባንክ እና በጋዛ ሰርጥ ለመመስረት ነው። ዋና ከተማውንም ምስራቅ እየሩሳሌም ለማድረግ አላማው አድርጐ የተነሳ ድርጅት ነው፡፡ የድርጅቱ መስራቾች ሼክ አህመድ ያሲን አብደላ ዓዘዚ እና መሐመድ ዘሐር ሲሆኑ የተመሰረተው በ1987 ዓ.ም ነው፡፡ ዋና መቀመጫውም በፍልስጤም እና በደሃ ኳታር ይገኛል፡፡ ድርጅቱ ኢስላማዊ መንግስት በፍልስጤም ከመመስረት ባሻገር የፍልስጤም ስደተኞችን ወደ እስራኤል መመለስና የ1967ትን ስምምነት መሰረት ያደረገ የድንበር ማካለልን አላማ አንግቦ የሚንቀሳቀስ ነው፡፡
የሐማስ ወታደራዊ አንጃ ከመሳሪያ ግዢና አቅርቦት ጀምሮ እስከ ወታደራዊ ጥቃት የመፈፀም ተግባራትን ይፈፀማል፡፡ እንደ እስራኤል የስለላ ድርጅት መረጃ መሰረት፤ ሀማስ አባላቱን የሚያሰለጥነው በኢራንና በሶሪያ ውስጥ ነው፡፡ ሐማስ በዚህ አንጃው አማካኝነት በርካታ የአጥፍቶ መጥፋት ፍንዳታዎች እንዲሁም የሞርታርና የሮኬት ጥቃቶችን በእስራኤል ላይ አድርሷል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ አንዳንዶቹን ለመጥቀስ፡- አፕሪል 9 ቀን 1996 በካፋር የአውቶብስ አጥፍቶ መጥፋት ፍንዳታ 8 ሰዎች ሲሞቱ፣ ሃላፊነቱን ሐማስ ወስዷል፡፡
ፌብሯሪ 25 ቀን 1996 በኢየሩሳሌም የአውቶብስ ላይ ጥቃት 26 ሰዎች ሲሞቱ፣ አሁንም ሃላፊነቱን ሀማስ ወስዷል፡፡
ማርች 3 ቀን 1996 ዓ.ም አሁንም በኢየሩሳሌም ባደረገው የአጥፍቶ ማጥፋት ፍንዳታ 19 ሰዎች ሲሞቱ፣ እስራኤል ከሐማስ ራስ አልወረደችም፡፡
ማርች 4 ቀን 1996 በዲዝ ንግፍ ሴንተር በደረሰው ፍንዳታ 13 ሰዎች ሲሞቱ፣ ሐማስና ኢስላማዊ ጀሃድ ዋናዎቹ ተጠያቂዎች ነበሩ፡፡
ይህ እንግዲህ በአንድ አመት ውስጥ ብቻ ያደረሰው ጥቃት ሲሆን ከ1996-2014 ያደረሰው ጥቃት ምን ያህል ሊሆን እንደሚችል መገመት አያዳግትም፡፡
በ2007 በተካሄደው ጥናት መሰረት፤ እስራኤል ላይ ከተደረጉት የአጥፍቶ መጥፋት የቦንብ ፍንዳታዎች 39.9 ፐርሰንቶቹ በሐማስ የተደረጉ ሲሆን 26.4 በፋታህ፣ 25.7 በኢስላሚክ ጀሀድ፣ 5.4 በፍልስጤም ነፃ አውጭ ግንባር (PFLP) 2.7 ደግሞ በሌሎች ድርጅቶች የተደረጉ ናቸው፡፡ IZZad al quassam” በመባል የሚታወቀው የሐማስ ወታደራዊ ክንፍ የተመሰረተው እ.ኤ.አ በ1992 ዓ.ም እንደሆነ ይታወቃል፡፡
መጅሊስ አል ሹራ ወይም የምክር ቤቱ መቀመጫ በሐማስ ውስጥ ከፍተኛ ስልጣን ያለው አካል ሲሆን ስብስቡም ከዌስት ባንክ፣ ከጋዛ፣ ከእስራኤል እስር ቤትና ከፖለቲካ ቢሮ በተውጣጡ አባላት የተዋቀረ ነው፡፡ ምክር ቤቱ ከሚዲያ ፕሮፖጋንዳ እስከ ወታደራዊ ጥቃት ያሉትን እንቅስቃሴዎች ይወስናል። ከፍተኛው ውሳኔ ሰጪ አካል ግን የፖለቲካው ቢሮ ነው፡፡
በ2014 የሐማስ የፖለቲካ ቢሮ ምክትል ሊቀመንበር ሙሳ አህመድ አቡ መዝሩቅ፤  “ሐማስ እስራኤልን እንደ ሐገር እውቅና አይሰጥም” ብለው ነበር፡፡ ይህ የማይሻገሩት ቀይ መስመር ነው፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

“...ማህበረሰቡ በጣም እንደብርቅና እንደአስደንጋጭ ነገር ሊያየው ይችላል፡፡ እኔ ግን ከሙያ አንጻር በተደጋጋሚ የገጠመኝ ነገር አለ፡፡ ይኄውም የወንዶች ልጆች ተገዶ መደፈር ጉዳይ ነው፡፡ የወንዶች ልጆች ተገዶ መደፈር ሲባል ወንዶች በወንዶች የሚፈጸምባቸው ግብረሰዶማዊ ድርጊት እንዳለ ሆኖ እና ይህንንም ህብረተሰቡ በተቻለው መጠን በንቃት የሚከላከለው ድርጊት ሲሆን ከዚህ ውጭ ግን ወንዶች በሴቶች የሚደፈሩበት ሁኔታ አሰቃቂ ወይንም አስደንጋጭ እየሆነ ነው፡፡ ሁኔታው አጋጥሞ የተደፈሩት ሕጻናት ወደሆስፒታል ሲመጡ ሐኪሞቹ ጭምር እጅግ እያዘኑ ነው...”
                            መኮንን በለጠ የስነልቡና ባለሙያ
ከላይ ያነበባችሁት ገጠመኝ ባለፈው ሳምንት ለንባብ ብለነው ያልተቋጨው በአዳማ እየደረሰ ያለውን ተገዶ የመደፈር ሁኔታ ቀጣይ ጽሁፍ ነው፡፡ በዚህ አምድ የስነልቡና ባለሙያው አቶ መኮንን በለጠ እና በአዳማ የአቃቤ ሕግ ባለሙያዋን ብርቱካን እሸቱን ቀሪ ሀሳብ እናስነብባችሁዋለን፡፡ አቶ መኮንን በስራ አጋጣሚያቸው ያዩትን ሰዎች በወንድም ይሁን በሴት ሕጻናቱ ላይ የሚያደርሱትን አሰቃቂ ድርጊት ለጥንቃቄ ይረዳ ዘንድ በዚህ እትም ለንባብ ብለነዋል፡፡
“...አንድ የአራት አመት ህጻን ልጅ እቤት ውስጥ በተቀጠረች ሴት ሰራተኛ ተገዶ ተደፍሮአል፡፡ የሰራተኛዋ እድሜ ወደ ሀያ አራት ወይንም ሀያ አምስት አመት  የሚደርስ ነው፡፡ ሕጻኑ በተደጋጋሚ ወደ ሆስፒታል እየመጣ ሲታከም በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎች ተገኝቶበታል፡፡ ልጁ በምን መንገድ እንደተደፈረ እንዲያሳይ የተለያዩ አሻንጉሊቶች ቀርበውለት ነበር፡፡ በአሻንጉሊት እንዳሳየው ከሆነ ማንኛውም ወንድና ሴት የግብረስጋ ግንኙነት በሚፈጽሙበት መንገድ መሆኑን ለሐኪሙም ለሌሎችም ባሙያዎች በግልጽ አሳይቶአል፡፡...”
አቶ መኮንን እንደገለጹት ህጻናት ካሜራዎች ናቸው። ማንኛውንም የተፈጸመባቸውን ድርጊት  በባለሙያ አማካኝነት በተለያየ መንገድ እንዲያሳዩ በሚጠየቁበት ጊዜ በግልጽ ያሳያሉ፡፡ ተገደው የተደፈሩ ህጻናት በአንድ ቦታ ሁሉንም አገልግሎት ከሚያገኙበት ክፍል በአሻንጉሊት እንዲሁም ስእል በመስራትና በተለያዩ መንገዶች የደረሰባቸውን በደል ሁሉ ካለፍርሀት እንደሚገልጹ አቶ መኮንን አስረድተዋል፡፡
“...ታሪኩ የተገለጸው የአራት አመት ልጅ በብልት አካባቢው የመቅላት፣ የመፈግፈግ እንዲሁም የማበጥ ሁኔታ እንደደረሰበት ያዩት ሰራተኛዋ አሰናብቱኝ ብላ ከሄደች በሁዋላ ነው፡፡ ልጁ ወደሆስፒታል ሲመጣ እጅግ አስደንጋጭ እንዲሁም አሳዛኝ ሁኔታ ነበረው። በአሁኑ ጊዜ በተለያዩ ምክንያቶች በተለይም በስራ አጋጣሚ ልጆቻቸውን ለሞግዚት ወይንም ለጠባቂ ጥለው የሚሄዱ ወላጆች በርካታ ናቸው፡፡ ያ ማለት ግን ልጆችን ሙሉ በሙሉ ለሞግዚት ትቶ ክትትል ማድረግ አያስፈልግም ማለት አይደለም፡፡ ወላጆች ለልጆቻቸው  በተቻለ መጠን ተገቢውን ክትትል ማድረግ፣ ገላቸውን መፈተሽ እንዲሁም በግልጽ ማነጋገር፣ ማጫወት፣ ልጆቹ ሃሳባቸውን እንዲገልጹ ማድረግ ይገባቸዋል...”
አቃቤ ሕግ ብርቱንን እሸቱ በአዳማ ተገዶ መደፈር እየጨመረ ወይንም እየቀነሰ ነው ለማለት ያስቸግራል ብላለች፡፡ እንደ ብርቱካን፡-
“...አንዳንድ ጊዜ ህብረተሰቡ የደረሰውን ጥቃት ለህግ ወይንም ለሕክምናው ተቋም በግልጽ ማሳወቅ አይፈልግም፡፡ ከአሁን በፊት ስለሁኔታው ለማስተማር ሙከራ ሲደረግ ተገዶ የመደፈር ጥቃት ሊደበቅ ወይንም በሽምግልና ሊያልቅ የሚገባው ነገር እንዳልሆነ ለህብረተሰቡ ግልጽ ለማድረግ ተሞክሮአል፡፡
የዚህም ምክንያቱ ወንጀለኛውን ወደህግ ከማቅረብ ባሻገር ተገደው የተደፈሩት ሴቶችም ይሁኑ ወንዶች ልጆች ከሚደርስባቸው አካላዊ እና ስነልቡናዊ ጉዳት እንዲያገግሙ ወይንም ወደትክክለኛው መንፈሳቸው ተመልሰው ህይወታቸውን በጥሩ መንፈስ እንዲቀጥሉ የሚያስችላቸውን ሕክምናና የስነልቡና ድጋፍ እንዲያገኙ ያስችላል ከሚል ነው፡፡
ይህ ካልሆነ ግን በልጆቹ ላይ ጉዳት እንደሚደርስ የተነገረ ቢሆንም አሁንም ብዙዎች በሽምግልና ጉዳዩን እየያዙ ወደ ህግ ስለማይቀርቡ ሁኔታው በዚህ ደረጃ ላይ ነው ለማለት ያስቸግራል፡፡ ይሁን እንጂ ብዙ ወላጆች ሽምግልናውን አንቀበልም እያሉ ልጆቻቸውን ስለሚያመጡ እና ስለሚያሳክሙ ልጆቹም ወደጥሩ ሁኔታ ይመለሳሉ፡፡ አጥፊዎችም ካደረሱት ጥፋት አንጻርና ፌደራል ያወጣውን የቅጣት ማኑዋል መሰረት በማድረግ ከአምስት አመት እስከ ሀያ አምስት አመት የሚያስቀጣ ይሆናል...”
በአዳማ ሆስፒታል ግቢ ውስጥ በሚገኘው ጥቃት የደረሰባቸው ሕጻናት ሁሉንም አገልግሎት በሚያገኙበት ክፍል በስነልቡና ባለሙያነት የሚሰሩት አቶ መኮንን በለጠ አንድ ታሪክ ነግረውናል፡፡
“...ልጅትዋ በእንጀራ አባትዋ ተገዳ ትደፈራለች። እናትየው  በመጀመሪያ ስሜታዊ ሆና ወደ ህግ ፍለጋ ከመጣች በሁዋላ በሽምግልና ስትያዝ ግን ልጅትዋን ወደመደበቅ ታመራለች፡፡ ነገር ግን በአካባቢዋ የነበሩ ሰዎች ይህ መሆን እንደሌለበት ቢያስረዱዋትና ቢመክሩዋትም መቀበል ስላልቻለች ለፖሊስ ያመለክታሉ፡፡ በሁዋላም ልጅትዋን ከተደበቀችበት ቦታ አውጥተው ወደህግ ስላቀረቡዋት ልጅትዋ በሕጻናት ማቆያ እንድትገባ ተደርጎ ወንጀል የፈጸሙት ሰዎች ላይ አስፈላጊው የህግ እርምጃ ተወስዶአል፡፡
ወላጅ እናት ልጅዋ እሱዋ ባገባችው ለልጅቷ እንጀራ አባት በሆነው ሰው ስትደፈር ለጥቅምዋ ስትል የህግ እርምጃው ተቋርጦ ወደ ሽምግልና ለመዞር ማሰብዋ በጣም የሚያሳፍር እና የሚያሳዝን ነገር ነው...”  
ተገደው የተደፈሩ ልጆች የሚደርስባቸው የስነልቡና ችግር፡-
ራስን መቆጣጠር አለመቻልና ራስን አቅመ ደካማ አድርጎ ማየት
መቆጣትና በቀላሉ መበሳጨት
እንደገና ወሲባዊ ጥቃት ይከሰትብኛል ብሎ መፍራት
ፆታዊ ጥቃት ከደረሰባቸው ቦታ ለመሰወር ማሰብ
በሌላ ሰዎች ላይ ያላቸውን አመኔታ ማጣት
ስለወደፊቱ ያላቸው አመለካከት መደብዘዝ
ራስን አንቋሾ ማየት
ራስን ከህብረተሰብ ማግለል
ከዕለት ተዕለት ኑሮ ራስን ማግለል
ግብረስጋ ግንኙነት እና የአካላዊ ግንኙነት ማድረግ መፍራት
ግራ መጋባት
በቀላሉ መርሳት
ለስራዎች ትኩረት አለመስጠት
ቅዠት
እንቅልፍ ማጣት እና የአመጋገብ ስርአት መታወክ
ራስን ለመከላከል አላስፈላጊ እና የተጋነነ ዝግጅት ማድረግ
ስለደረሰው ችግር ራስን እንደ ጥፋተኝነት መኮነን እና መጨነቅ
የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ካወጣው እትም
ተገድዶ መደፈር በማንም ላይ ሊደርስ የሚችል ወሲባዊ ጥቃት ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ችግር ሙሉ በሙሉ መወገድ የሚገባው ነው፡፡ ስለዚህ ምን ማድረግ ይገባል የሚል ጥያቄ ለስነልቡና ባለሙያው አቶ መኮንን በለጠ እና ለአቃቤ ህግ ባለሙያ ብርቱካን እሸቱ ተሰንዝሮአል፡፡
“...እኔ እንደባለሙያ የምገልጸው ነገር... ቤተሰብ እንዲሁም ህብረተሰብ ባጠቃላይም የሚመለከታቸው ክፍሎች ሕጻናቱን አስቀድሞ በማስተማር እንዲሁም ተገቢውን እንክብካቤ በማድረግ በቅርበት ክትትል የሚያደርጉበት ዘዴ ሊኖር ይገባል፡፡ ህጉ አስተማሪነቱ እና ፍትህን ለሚሹ እርካታ መሆኑ ባይካድም የህጻናትን ተገዶ መደፈር ለማስቀረት ፊት ለፊት የመጡ ነገሮችን ወደህግ በማቅረባችን እና በማስወሰናችን ብቻ ችግሩ የሚፈታ አይደለም፡፡ ህብረተሰቡ የበኩሉን ጥንቃቄ ማድረግ የሚጠበቅበት ሲሆን ከአቅም በላይ በሆነ መንገድ ችግሩ ከተከሰተ ወደህግ ሳይውል ሳያድር በፍጥነት ቢያቀርቡ አጥፊው ለሌሎች ማስተማሪያ የሚሆነውን ተገቢውን ውሳኔ ያገኛል፡፡ ስለዚህ ህብረተሰቡ ችግሩ ሲደርስበት ወደሽምግልና በመሄድ ጉዳቱን በመደበቅ በተለይም በህጻናቱ ላይ የሚያደርሰውን ተጽእኖ ማስቀረት ይገባዋል።
አቃቤ ሕግ ብርቱንን እሸቱ
“...ሕብረተሰቡ መገንዘብ ያለበት ነገር ሰው ከሰው ምን ያህል እንደሚለያይ ነው፡፡ አንዱ ስለታመነ ሌላውም መታመን እንደሌለበት መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ወላጆችን በሚመለከትም ለልጆቻቸው ከፍተኛ መስዋእትነትን የሚከፍሉ የመኖራቸውን ያህል አንዳንዶች ደግሞ ዘወር ብለው የማይመለከቱ እንደሆኑ ከየእለት ተእለት ገጠመኞች የምናየው ነው፡፡ ልጅ መውለድ ቀላል ነው። ወልዶ በስነስርአቱ በተገቢው መንገድ ማሳደግ እና ከሚፈለገው ደረጃ ማድረስ ግን ፈታኙ ነገር ነው፡፡ ስለዚህ ወላጆች ልጆቻቸውን ሲወልዱ በምን መንገድ ሊያሳድጉ እንደሚገባቸው ጠንቅቀው ሊያውቁ እንደሚገባቸው መልእክቴን ማስተላለፍ እፈልጋለሁ፡፡
አቶ መኮንን በለጠ (የስነ ልቡና ባለሙያ)    

Published in ላንተና ላንቺ

በአገራችን የሚከበሩ መንፈሳዊና ብሄራዊ ፌስቲቪሎችን የሚያስቃኝ “የኢትዮጵያ ፌስቲቫል ማውጫ” የተሰኘ መፅሀፍ ሰሞኑን ታትሞ የወጣ ሲሆን በነፃ እንደሚሰራጭ ታውቋል፡፡ መፅሀፉ ከ15 በላይ የመስቀል በዓል አከባበሮች፣ በተለያዩ አምስት አካባቢዎች የሚካሄዱ የጥምቀት በዓላት፣ የገና፣ የመውሊድ እና የአረፋ እንዲሁም የአሸንዳ፣ የእሬቻና ፍቼ በዓላትን ጨምሮ በርካታ ፌስቲቫሎችን ያካተተ ሲሆን፤ በዓላቱ መቼና እንዴት እንዲሁም ለምን እንደሚከበሩ መረጃ ይሰጣል፡፡ ማውጫው ለሀገር ውስጥ ጎብኚዎች፣ ተመራማሪዎች፣ ለመገናኛ ብዙሃንና ለአስጎብኚዎች በነፃ ይሰራጫል ተብሏል፡፡

በደራሲ ወንድሙ ነጋሽ የተፃፈው “የአዕምሮ ጉዳይ” የተሰኘ መፅሃፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ አዕምሯችን የማናውቀው ፕላኔት ነው የሚለው መፅሃፉ፤ ስለ አእምሮ ህመምና ማህበረሰቡ ለአእምሮ ህመምተኞች ስላለው አመለካከት፣ ለአዕምሮ መታወክ መንስኤ ስለሚሆኑ ጉዳዮችና መፍትሄዎቻቸው… የሚዳሰስስ ነው፡፡ በ192 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ39 ብር ከ60  ለገበያ የቀረበ ሲሆን የመፅሀፉ ሽያጭ ገቢ በአዕምሮ ህመም ለሚሰቃዩ ወገኖች ለሚቋቋመው ድርጅት መርጃ ይሆናል ተብሏል፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም “የአዕምሮ አስተዳደር ሞዴል” እና “ፍቅር ምንድን ነው” የሚሉ መፃህፍትን ለአንባቢያን ማድረሳቸው ይታወቃል፡፡

በባህላዊ የማሲንቆ አጨዋወቱ ተወዳጅነትን ያተረፈው አርቲስት ተስፋፅዮን ገ/መስቀል “ጀመረኒ” የተሰኘ አዲስ አልበም ለገበያ አቀረበ፡፡ በ “ዶን ፊልሞች” ፕሮዱዩስ የተደረገው አልበሙ፤ የሰርግ ዘፈንን ጨምሮ 13 ባህላዊ የትግርኛ ዘፈኖችን የያዘ ሲሆን “ዳ’አማት መልቲ ሚዲያ” አሳትሞ እያከፋፈለው ነው፡፡ ድምጻዊው ከዚህ ቀደም “ቆልዑ ገዛና” የተሰኘ ተወዳጅ አልበም ማውጣቱ የሚታወቅ ሲሆን በአሜሪካ፣ በአውሮፓና በመካከለኛው ምስራቅ አገራት ለሚገኙ ኢትዮጵያውያን አድናቂዎቹ ኮንሰርት ማቅረቡ ታውቋል፡፡