የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋልያዎቹ የብራዚል ጉዞ  በ20ኛው ዓለም ዋንጫ  ተሳትፎ  ባይሳካም፤ ለሁለት ሳምንት ዝግጅት መሄዳቸው አልቀረም፡፡
በአሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ጥረት በብራዚል በካምፕ በአይነቱ የተለየ ዝግጅት የሚያደርጉት ዋልያዎቹ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ  ተሳታፊነት ብራዚልን በመርገጥ አስደናቂ ብቃት ያሳየችውን አልጄርያ ከመግጠማቸው በፊት ጥሩ ብቃት ላይ እንደሚደርሱ እየተነገረ  ነው፡፡ ከብራዚል ክለቦች ጋር የወዳጅነት ጨዋታ የሚያደርገው ብሄራዊ ቡድኑ  በቆይታው የሚያገኘው ጥቅም ያመዝናል። አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ቋሚ ተሰላፊ ቡድናቸውን ለመለየት ያሰቡ ይመስላል፡፡ ባሬቶ በሃላፊነቱ በቆዩባቸው ጊዜያት ቋሚ አምበል አለመሾማቸው ሙሉ ቋሚ ተሰላፊዎች አለመለየታቸውን ያመለክታል፡፡ ፍቅሩ ተፈራ፤ አበባው ቡጣቆ እና ፍፁም ገብረማርያም አምበሎች እንደሚሆኑ እየተገመተ ነው፡፡ አዳነ ግርማ፤ ሳላዲን ሰኢድና መስኡድ መሃመድም ለሃላፊነቱ ብቁ መሆናቸውም ይገለፃል፡፡ 19 አባላትን ያካተተው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን  የመጀመርያው ልዑክ ረቡዕ ወደ ብራዚል ተጉዟል፡፡ ቀሪዎቹ ዛሬ ይበራሉ፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በብራዚል በሚኖረው የ14 ቀናት ቆይታ 33 አባላት ያሉት ልዑክ ይኖረዋል። በብራዚሊያ የሚገኘው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በነገው ዕለት ከሰሜን ብራዚል ከመጣው ሬምዋ ከተባለ ክለብ ይጫወታል፡፡ የዛሬ ሳምንት ደግሞ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ጨዋታ አስተናግዶ በነበረው የማኔ ጋሪንቻ ስታድዬም ሁለተኛውን ጨዋታ ያደርጋል፡፡  ከ2 ሳምንት በኋላ  ደግሞ ሬዮ ግሬምዬ ከተባለ ክለብ ጋር ሶስተኛውን የወዳጅነት ጨዋታ ያደርጋል፡፡ ሦስቱም የብራዚል ክለቦች በአገሪቱ የክለብ ውድድር በ4ኛ ዲቪዚዮን የሚጫወቱ ናቸው፡፡ ጨዋታዎቹ አቋምን ከመፈተሽ ባሻገር ተጫዋቾቹን ለማስተዋወቅ ጥሩ እድል እንደሚፈጥር አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ተናግረዋል፡፡
በ2015 እኤአ ላይ ሞሮኮ ለምታስተናግደው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ በሚካሄድ  የምድብ ማጣርያ የሚሳተፈው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከአልጄርያ ጋር  ከመጫወቱ በፊት ቢያንስ ስምንት የወዳጅነት ጨዋታዎች ሊያደርግ ይችላል፡፡ ዋልያዎቹ ባለፈው ሰሞን  በሉዋንዳ ላፓላንካ ኔግራስ ከተባለው የአንጎላ ብሄራዊ ቡድን ጋር በመጀመርያ የወዳጅነት ጨዋታቸው ተገናኝተው 1ለ0 ተሸንፈዋል፡፡
በሉዋንዳ 11 ዲ ኔቨምብሮ ስታድዬም በተደረገው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ አንጎላ ያሸነፈችው ፍሬዲ የተባለ ተጨዋች በ16ኛው ደቂቃ ላይ ባገባት ብቸኛ ግብ። የአንጎላው ፕሬዝዳንት ጆሴ ኤድዋርዶ ዶሳንቶስ የክብር እንግዳ ነበሩ፡፡
ከብራዚል መልስም  በነሀሴ ወር ሁለት የደርሶ መልስ የወዳጅነት ጨዋታዎችን ፈርኦኖቹ ከተባለው የግብፅ ብሄራዊ ቡድን ጋር ለማድረግ ቀጠሮ መያዙም አስታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በምድብ 2 የመጀመርያ የማጣርያ ጨዋታው ጳጉሜ 2 ላይ በአዲስ አበባ ስታድዬም ከአልጄርያ  ይገናኛል፡፡ አልጄርያና ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ የማጣርያ እና ዋና ውድድሮች 6 ጊዜ ተገናኝተዋል። እኩል አንዴ ተሸናንፈው በ4 ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል፡፡ በምድብ 2 ከአልጄርያ፤ ከማሊ እና ከኢትዮጵያ ጋር ማጣርያ የምትገባው አራተኛ ቡድን ማላዊ ሆናለች፡፡ ማላዊ ምድቡን የተቀላቀለችው በሁለተኛ ዙር ቅድመ ማጣርያ ቤኒን ጥላ በማለፍ ነው፡፡
በተያያዘ ዜና የሴካፋ ዋና ፀሃፊ ኒኮላስ ሙንሶኜ በሞሮኮው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመካከለኛው እና የምስራቅ ዞን አንድ ተወካይ መኖሩ አይቀርም ብለዋል። ከዞኑ አራት ቡድኖች በምድብ ማጣርያው የሚካፈሉ ሲሆን ኢትዮጵያ እና ሱዳን በቀጥታ ወደ ምድብ ሲገቡ በቅድመ ማጣርያ ያለፉት ደግሞ ሩዋንዳ እና ኡጋንዳ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ በማጣርያ  በሜዳዋ በምታደርጋቸው ጨዋታዎች ባለፈው ሁለት ዓመት ያሳየችው ብቃት ለጥንካሬዋ ምክንያት እንደሚሆን ኒኮላስ ሙንሶኜ ገልፀዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከወራት በኋላ የመካከከለኛው እና ምሰራቅአፍሪካ ሻምፒዮና አዘጋጅ እንደሆነች ይታወቃል።

ሰሞኑን ባልተጠበቀ የአስተዳደር ችግር እየተናጠ ያለው ኢትዮጵያ ቡና በካጋሜ ካፕ አለመሳተፉ ትልቅ ኪሳራ ነው ማለት ይቻላል፡፡ በክፍለ አህጉራዊው የክለቦች ሻምፒዮና  ያልተሳተፈበት ምክንያት ከተፈጠረው ችግር ከተያያዘ የሚያሳዝን ነው፡፡ ካጋሜ ካፕ የክለቡን ብራንድ የሚያሳድግ ውድድር ነበር፡፡ ለሚቀጥለው የፕሪሚዬር ሊግ የውድድር ዘመን ከፍተኛ መዘጋጂያ ሊሆን የሚችልም ነበር፡፡
የ27 ዓመቱ ዳዊት እስጢፋኖስ በአማካይ ተጨዋችነት ምርጥ ከሚባሉ ዋልያዎች ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ነው፡፡ የታላቁ ክለብ ኢትዮጵያ ቡና አምበል እና ወሳኝ ተጨዋች ሆኖ የሚያገለግለው ዳዊት፤ ከዋልያዎቹ ጋር ወደ ብራዚል የመሄድ እድል አልገጠመውም። በጉዳት ላይ ሲሆን እያገገመ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ቡና ውስጥ ሰላም እንዲሰፍን ጥሪ የሚያቀርበው ዳዊት ዋልያዎቹ ከማርያኖ ባሬቶ ጋር እየሰሩ ያሉት ዝግጅት ከሞላ ጎደል ጥሩ ብሎታል፡፡ በተጨዋቾች ዝውውር ገበያ ደህና ክፍያ መሰማቱን ደግሞ የስፖርቱ እድገት መገለጫ መሆኑን ገልጿል፡፡ የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ ዳዊት እስጢፋኖስን ለቀጣይ 2 ዓመት ኮንትራቱን እንዲያራዝም የከፈለው 1.2 ሚሊዮን ብር ነው ፡፡  በኢትዮጵያ እግር ኳስ የተጨዋቾች ዝውውር ገበያ አዲስ ሪኮርድ የፊርማ ሂሳብ ተብሏል፡፡  የብሄራዊ ቡድን ተጨዋች  አይናለም  ሃይሉ ከዓመት በፊት ከደደቢት ክለብ ወደ ዳሸን ቢራን የተቀላቀለበት  1.1 ሚሊዮን ብር ቀድሞ የተመዘገበው ሪከርድ ክፍያ  ነበር፡፡
ከውጭ አገር ክለቦች የባርሴሎና  እና አርሰናል ክለቦችን አደንቃለሁ የሚለው ዳዊት እስጢፋኖስ በእረፍት ጊዜው ከብዙ ጓደኞቹ ጋር ተሰባስቦ በሁሉም ጉዳይ መጫወት ያስደስተኛል ብሏል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ፊልሞችን በመከታተል እየተመለከተ ነው፡፡
ዳዊት እስጢፋኖስ ከስፖርት አድማስ ጋር ያደረገው አጭር ቃለምልልስ ከዚህ በታች የቀረበው ነው፡፡    
ስለ ኢትዮጵያ ቡና ወቅታዊ ሁኔታ
ለማንም ወገንተኛ በመሆን የምናገረው ነገርየለም። እኔም የቡና ነኝ ፤እነሱም የቡና ናቸው፡፡ የሁላችንም ለሆነው ታላቅ ክለብ ብለው በቶሎ ያለባቸውን ልዩነት አጥብበው በቶሎ መስማማታቸውን በጉጉት እጠብቀዋለሁ፡፡
ስለ የአሁኑ ብሄራዊ ቡድንና ማርያኖ ባሬቶ
 ከብሄራዊ ቡድኑ ጋር በሰራሁባቸው ቀናት የታዘብኩት በጣም ጥሩ ደረጃ ላይ እንደምንገኝ ነው፡፡ አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶን በሁለት ነገር አደንቃቸዋለሁ። በቡድኑ ተጨዋቾች የአካል ብቃት ላይ በማተኮር መስራታቸው ለውጥ ነበረው፡፡ በሌላ በኩል የወዳጅነት ጨዋታዎችን መተግበር የቻሉ አሰልጣኝ ናቸው፡፡ አስቀድሞ በነበረው የብሄራዊ ቡድን ዝግጅት የወዳጅነት ጨዋታዎች ብዙም የሚሳኩ አልነበሩም፡፡
በአጠቃላይ በታክቲክ እና በአካል ብቃት የሚሰሩ ስልጠናዎች እድሜያቸው ለገፋ 25 እና ከዚያም በላይ ለሆኑ ተጨዋቾች በብሄራዊ ቡድን ደረጃ ለመስራት አድካሚ ይመስለኛል፡፡ ይህ ሁኔታ ከታዳጊዎች ተነስቶ በመስራት በሁለት እና ሶስት ዓመት ለውጥ የሚታይበት ነው፡፡ ይህ ቡድን በጣም አብሮ የቆየ ነው፡፡ በመሰረታዊ ነገር መጎተት የለበትም፡፡ የወዳጅነት ጨወቃታዎቹን በተመለከተ ግን እሰከዛሬ የማይሳካው አሁን መገኘቱ ጥሩ ርምጃ ነው፡፡ ለወደፊቱ ግን የወዳጅነት ጨዋታዎቹ በጥናት መደረግአለባቸው፡፡ በገባንበት ፉክክር በሚገጥሙን ቡድኖች አቋም እና የኢትዮጵያዊያን ተጨዋቾች ያላቸውን አቅም ተተንተርሶ የወዳጅነት ጨዋታ መዘጋጀት አለበት፡፡ የተጋጣሚ አገር ሜዳ እና የራስ ሜዳ ሁኔታ እና አየር በማጥናት የሚደረግ ዝግጅትን የሚያግዝ የወዳጅነት ጨዋታ ያስፈልጋል፡፡
ስለ ምድብ 2
የምድብ ማጣርያው ላለፈውአፍሪካ ዋንጫ ከነበረው ድልድል ይከብዳል፡፡ በራሳችን አጨዋወት ጠንካራ ተፎካካሪ መሆን እንችላለን፡፡ በተለይ በሜዳችን ለምናደርጋቸው ጨዋታዎች ትኩረት መስጠት አለብን፡፡ በጠንካራ ብሄራዊ ስሜት በመስራት ውጤታማ ለመሆን የተነሳሳን ይመስለኛል፡፡ በስነልቦና የምናደርገው ዝግጅትም ወሳኝ ይሆናል፡፡
ስለ ተጨዋቾች የዝውውር ገበያ
ከቅርብ ዓመታትወዲህ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ማደጉ በተለያየ መንገድ ይገለፃል፡፡ አንዱ መገለጫ ደግሞ የተጨዋቾች የዝውውር ገበያው በከፍተኛ ሂሳብ መካሄዱ ነው፡፡ ካለፉት አራትአመታት ወዲህ ተጨዋቾች በብቃታቸው ተፈላጊ ሆነው ከክለብ ወደ ክለብ ለመዘዋወር የሚያገኙት የፊርማ ሂሳብ ተጠቃሚ እያደረጋቸው ይገኛል፡፡ተጨዋቾች በክለባቸው ልምምድሰርተው በግላቸውም ብቃታቸውን ለማሳደግ የሚጥሩበት ጊዜ ላይ ነን፡፡ 1 ሚሊዮን ብር እየተከፈለ ማንም የሚተኛ የለም፡፡ የስፖርቱ እድገት በኢኮኖሚ በሚኖሩ መሻሻሎች የሚፋጠን ይመስለኛል፡፡


ብዙ ሰዎች ለሕጻናት ተገቢውን እንክብካቤ የሚያደርጉ ቢሆንም አንዳንዶች ግን ባልተጠበቀ እና ባልተገመተ ሁኔታ ጥቃት ሲፈጽሙ ይታያሉ፡፡
መኮንን በለጠ (የስነልቡና ባለሙያ)
የወሲብ ጥቃት በአንድ ሰው ላይ ብቻ የሚደርስ ችግር ሳይሆን በማንም ግለሰብ (በወንዶች፣ በሴቶች፣ ትንንሽ ወንድ ልጆች፣ ልጃገረዶች) ሊፈጸም ይችላል። ይህ... መደፈር የደረሰበት ሰው ያመጣው ችግር አይደለም፡፡
ከላይ ያነበባችሁት መረጃ የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ቀደም ሲል ካሳተመው ዶክመንት የተወሰደ ነው፡፡ ተገድደው የሚደፈሩ ሰዎች በአንድ ማእከል አገልግሎት የሚያገኙበትን አሰራር ለመመልከት ወደ አዳማ ሆስፒታል ተጉዘን የተለያዩ እውነታዎችን ይዘን ተመልሰናል፡፡ ከእውነታዎቹም መካከል ልጆቻቸው ተገድደው የተደፈሩባቸው አንዲት እናት እና አንድ አባት ይገኙበታል፡፡ የአቃቤ ሕግ እና የስነልቡና ባለሙያም ሀሳባቸውን ለዚህ እትም አካፍለዋል፡፡
አቃቤ ሕግ ብርቱካን እሸቱ እንደገለጸችው “...አዳማ ሆስፒታል ውስጥ የሴቶችና የህጻ ናት (center) ማእከል በሚል የተከፈተው ክፍል ከፖሊስና ከሕክምና ባለሙያ እንዲሁም ከስነልቡና ባለሙያ ጋር በመሆን የሚደርሰውን ችግር በቅርበት ለመፍታት የሚቻልበት ነው፡፡ በዚህ ክፍል ሴቶች እንዲሁም ሴት ሕጻናት እና ወንዶችም ላይ የአስገድዶ መደፈር ጥቃት ሲደ ርስባቸው በፍጥነት ፍትሕ እና ሌሎችንም እርዳታዎችን የሚያገኙበትን አሰራር እንከተላለን፡፡ አንድ ችግር መድረሱ ከባለጉዳዮች ጥቆማ ሲደረግ ወዲያውኑ ፖሊስ ወደ አካባቢው በመዝለቅ ሁኔታውን ካጣራ በሁዋላ የባለጉዳዮችን ቃል እንዲሁም የአካባቢውን ምስክርነት እና የህክምና ማስረጃውን በመጨመር ጉዳዩ በሕግ እንዲያዝ እናደርጋለን፡፡ ብዙ ጊዜ ወላጆች ፈጥነው ለማመ ልከት ወደማእከሉ ስለማይመጡና በሽምግልና ጉዳዩን ደብቀው ይዘው ስለሚያድበሰብሱት ተዳፍኖ የሚቀር ቢሆንም በተለይም በአሁኑ ወቅት ብዙዎች የዚህን ክፍል መቋቋም እያወቁ በመሆናቸው እየቀረቡ ፍትሕ እያገኙ ነው፡፡ በእርግጥ አሁንም አንዳንድ መዘግየቶች በመኖራ ቸው ሕጻናቱ እየተጎዱ መሆኑን በዚሁ አጋጣሚ መልእክት ማስተላለፍ እንፈልጋለን...” ብላለች፡፡     
አቶ ረመዳን ደሊል የ6 አመት እድሜ ያላት ልጅ አባት ነው፡፡  
ጥ/    ወደአዳማ ሆስፒታል የመጣህበት ምንያት ምንድነው?
መ/    የ6 አመት እድሜ ያላት ሴት ልጄ ተገዶ የመደፈር ሙከራ ደርሶባት ነው፡፡
ጥ/    በምን አይነት ሰው ነው ሙከራው የተፈጸመው?
መ/    በእድሜ ትልቅ ሰው ነው፡፡ የሀይማኖት ተከታይ ወይንም አስተማሪ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ምናልባትም ችግር እንኩዋን ቢገጥመኝ ልጄን ጠብቅልኝ ብዬ አደራ ልሰጠው የምችለው የማምነው ሰው ነው ይህን ያደረገው፡፡
ጥ/    በልጅቷ ላይ የደረሰውን የመደፈር ሙከራ በምን መንገድ አወቅህ?
መ/    ለጉዳይ ከቤት ወጣ ብዬ ሰላሳ ደቂቃ እንኩዋን ባልሞላ ፍጥነት ስመለስ ከቤት የለችም፡፡ የት ሄደች ብዬ ተመልሼ ስወጣ ጫማዋን የመድፈር ሙከራ ካደረገው ሰውየ ቤት በራፍ ላይ አየሁት፡፡ አንቺ ምን እያደረግሽ ነው? ብዬ ወደቤቱ ስገባ ሰውየው እራሱን አያው ቅም፡፡ ልብሱን አውልቆአል፡፡ የሷንም ልብስ ገልጦ የሚችለውን ነገር አድርጎአል፡፡ እኔም በጩኸት ...አንተ የተከበርክ ትልቅ ሰው አይደለህም እንዴ? እንዴት ይህን ታደርጋለህ ብዬ መታሁት፡፡ ልጅቷንም ጭምር መታሁዋት፡፡
ጥ/    ልጅትዋን ለምን መታሀት?
መ/    እኔ ልጅቷን ያለእናት ነው የማሳድጋት።  ስለዚህም በጣም ጥበቃ እና ክትትል አደርጋለሁ። በቅድሚያ በተቻለኝ አቅም በእንደዚህ ያለ ሁኔታ ሊደርስባት ከሚችል አደጋ እራስዋን እንድትጠብቅ ሁሉንም ነገር ነግሬአት ወይንም አስረደስቼአት ነበር፡፡ ነገር ግን ያንን ከግንዛቤ አላስገባችውም ወይንም ሕጻን ስለሆነች አልገባትም ማለት ነው ይህ ችግር ተከስቶአል፡፡ሁኔታው ስላናደደኝ መታሁዋት፡፡
ጥ/    ቀጣዩ እርምጃህ ምንድን ነበር?
መ/    በመቀጠል በፍጥነት ሌላ ጎረቤት ጠርቼ ሰውየው እንዳያመልጠኝ ጠብቅልኝ... ከቤት እንዳይወጣ በማለት ፖሊስ ፍለጋ ነበር የሄድኩት፡፡ ፖሊስ አምጥቼም ሁሉንም ነገር አስረድቼ ወደህግ እንዲቀርብ አድርጌአለሁ።
ጥ/    ሕክምና አግኝታለች?
መ/    አዎን ...ሕክምና ተደርጎላታል፡፡ ነገር ግን የአካል መፈጋፈግ እንጂ ሕግዋ አልተወሰደም ብለውኛል።   
በአዳማ ሆስፒታል የተለየ ፍላጎት ላላቸው ሕጻናት አገልግሎት መስጫ ከሆነው ክፍል ውስጥ ያገኘናቸው የስነልቡና ባለሙያው አቶ መኮንን በለጠ በተከሰተው ጉዳይ የሚከተለውን አስተያየት ሰጥተዋል፡፡
“...የህጻናቱ መደፈር በየቀኑ በየሰአቱ የሚያጋጥመን ጉዳይ ነው፡፡ ችግሩ ለተከሰተባቸውም የህክምና አገልግሎት የህግ እና የምክር አገልግሎት የሚሰጥበት ሁኔታ በክፍሉ ተመቻችቶአል፡፡ ለቤተሰብ ወይንም ለማህበረሰብ ጥሩ ትምህርት ይሰጣሉ ከምንላቸው ጉዳዮች መካከል ከላይ አጋጣሚው የተነበበው ታሪክ አንዱ ነው፡፡ ምክንያቱም  ይህች የስድስት አመት እድሜ ያላት ሕጻን የመደፈር ሙከራ የደረሰባት የአካባቢው ሰው በሚያከብረው እና በሚያምነው የሃይማኖቱ አስተማሪ እንዲሁም ተጠሪ በሆነ ሰው አማካኝነት ነው፡፡ ይህ ገጠመኝ አስተማሪ ገጽታዎች አሉት፡፡
1/ የመድፈር ሙከራ ያደረገውን ሰው የልጅትዋ አባት አደራ የሚወጣ ሰወ ነው ብሎ ያመነው ሰው መሆኑ እና ልጅትዋም እንደአባት አምና የምትቀርበው ሰው መሆኑ... ነገር ግን በተቃራኒው ጥፋት መፈጸሙ ለሌሎችም እምነት እስከምን ድረስ ነው? የሚለውን ለመገመት የሚያስችል ነው፡፡ ይህ ገጠመኝ በአገርኛው አባባልም “... በሬ ከአራጁ...” እንደሚባለው ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ለሕጻናት ተገቢውን እንክብካቤ እና ጥበቃ የሚያደርጉ ቢሆንም አንዳንዶች ግን ባልተጠበቀ እና ባልተገመተ ሁኔታ ጥቃት ሲፈጽሙ ይታያሉ፡፡
2/ ልጅቷ የምታድገው በአባቷ ብቻ ሲሆን ለልጅቷ የሚያስፈልገውን እንክብካቤ በማድረግ ቅርበትን በመፍጠር አልፎ ተርፎም እንዳትጎዳ ሲል የተለያዩ ትምህርቶችን በመስጠት የሚሳድጋት ነው። አስቀድሞም ሰዎች በሴት ልጅ ላይ የሚያደርሱትን ጉዳት በሚመለ ከት አባትየው የቻለውን ያህል ለልጅቷ ማስረዳት ሞክሮአል። ሕጻንዋ ግን እንደአባት በምታየው እና በምታምነው ሰው ጥቃቱ ተሞክሮባታል፡፡ ይህንን ከግምት ስናስገባ ..እናት እና አባት ገንዘብን በማለም ተለያይተው ልጅን ከሚያሳድጉ ይልቅ ችግራቸውን የሚያስወገግዱበትን መንገድ በመፈለግ አብረው ቢያሳድጉ እንደሚመረጥ ነው፡፡ የልጆ ቹን እንክብካቤ እንዲሁም ደህንነት እና የወደፊቱን ውጤት ማስተካከል የሚቻለው በጋራ ሆነው ልጆቻቸውን ቢያሳድጉ መሆኑን ማንም አይክደው..፡፡  
3/ የልጅቷ አባት ችግሩን በፍጥነት ወደህግ ለማቅረብ የሞከረበት ሁኔታ እና ልጅቷንም በፍጥነት ወደሕክምናው ማምጣቱ ሌላው አስተማሪ ነገር ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ጥቃት ያደረሰውን ሰው ክብር ለመጠበቅ ሲሉ የልጅትዋን ጉዳት ወደጎን በማድረግ ጉዳዩን በሽምግልና ለመያዝ ቢሞክሩ እንኩዋን አሻፈረኝ ...ሕግ እንዳደረገ ያድርገኝ ብሎ ጥፋተኛውን ወደሕግ ለማቅረብ መሞከሩ እጅግ የሚያስመሰግነው ነው፡፡ አንዳንድ ወላጆች በልጆቻቸው ላይ እንደዚህ ያለው ችግር ከተከሰተ በሁዋላ በዝምድና፣ በሽምግልና እና በገንዘብ በመሳሰሉት በመያዝ ጉዳዩን ወደሕግ ወይንም ሕክምና ሳያቀርቡ ስለሚተው ልጆቹን ምን ያህል እንደሚጎዱዋቸው ከዚህ ተግባር መማር እንደሚችሉ አንጠራ ጠርም፡፡
...ለግንዛቤ እንዲረዳዎት የሚከተሉትን እውነታዎች ይመልከቱ፡-
አስገድዶ መድፈር በማንም ላይ (በወንዶች፣ በሴቶች፣ ትንሽ ወንድ ልጆች፣ ልጃገረዶች፣ በአዛውንቶች፣ በድሀዎች፣ በሀብታሞች...) ወዘተ በማናቸውም ዜጎች ወይንም የሀይማኖት ተከታዮች ሊደርስ ይችላል፡፡
ማንም ሰው በፍላጎቱ አይደፈርም፡፡ የፈለገውን ልብስ ቢለብስ፣ የትም ቦታ ቢሆን፣ ምንም ቢያደርግ፣ መድሀኒቶች ወይም መጠጥ ቢጠቀምም በፍላጎቱ የሚደፈር የለም፡፡
ሰዎች በሚያውቁአቸው ወይንም በማያውቋቸው ሰዎች ሊደፈሩ ይችላሉ፡፡
አስገድዶ መድፈር የኃይል የበላይነት እና ተጎጂውን በቁጥጥር ስር ለማዋል የሚጠቀሙበት መሳሪያ ነው፡፡
አንድ ሰው ተገድጄ ልደፈር ብሎ አይቀርብም። ጥቃቱ ደርሶበት ከሆነ ጥፋቱ ሙሉ በሙሉ የአስገድዶ ደፋሪው ነው እንጂ የተደፋሪው አለመሆኑን ግንዛቤ ውስጥ ማስገባት ይገባል፡፡
አስገድዶ መድፈር የሰው ልጆችን ሰብአዊ መብት የሚጥስ በመሆኑ ወንጀል ነው፡፡    (ምንጭ፡ ESOG)
ይቀጥላል

Published in ላንተና ላንቺ

         ቁልፍ መረጃዎችን እያወጣ በዓለማቀፍ ደረጃ ክፉኛ ሲያሳጣት የከረመውን ኤድዋርድ ስኖውደን የተባለ ግለሰብ አሳድዳ ለመያዝና ለመፋረድ ደፋ ቀና ማለቷን የቀጠለችው አሜሪካ፣ አሁን ደግሞ ከእሱ የባሰ የብሄራዊ ደህንነት መረጃዎቼን እየዘረፈ በማውጣት ጉድ የሚሰራኝ ሌላ ሚስጥር መንታፊ ግለሰብ መጥቶብኛል ስትል ባለፈው ረቡዕ በይፋ መናገሯን ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
ስኖውደን የሚያወጣቸውን መረጃዎች እያተመ ለንባብ በማብቃት የሚታወቀው ዘ ኢንተርሴፕት የተባለ የአገሪቱ ጋዜጣ፣ ባለፈው ማክሰኞም ከዚህ ማንነቱ ያልተገለጸ ግለሰብ ያገኘውን የአገሪቱ ብሄራዊ ደህንነት መረጃ ለንባብ ማብቃቱን ተከትሎ ነው የአሜሪካ መንግስት አሁንም ሌላ አዲስ መረጃ ዘራፊ እንደመጣበት ያመነው፡፡
ዘ ኢንተርሴፕት ለንባብ ያበቃው ጽሁፍ፣ በኦባማ የስልጣን ዘመን አሜሪካ በሽብርተኝነት ጠርጥራ የምትመዘግባቸው ግለሰቦች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱንና  የግለሰቦችን መረጃ በሚስጥር እያፈላለገች የመያዝና የመሰለል ስራዋን የበለጠ አጠናክራ መግፋቷን የሚያትት ነው ተብሏል፡፡
ጋዜጣው ግለሰቡ ያወጣቸው መረጃዎች አገሪቱ በሽብርተኝነት ጠርጥራ ከመዘገበቻቸው ዜጎች ውስጥ 40 በመቶ ያህሉ ከአሸባሪ ቡድኖች ጋር ምንም አይነት ግንኙነት እንደሌላቸው የሚያረጋግጡ ናቸው ማለቱን የጠቆመው ዘገባው፣ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት ግን ጋዜጣው ወጡ የተባሉትን የሚስጥር መረጃዎች በአግባቡ ካለመረዳት የተሳሳተ ድምዳሜ ላይ መድረሱን  መናገራቸውን  አስረድቷል፡፡
ማንነቱ ባልተገለጸው ግለሰብ አማካይነት ወጡ ያላቸውን መረጃዎች ጠቅሶ ጋዜጣው እንዳስነበበው፣ አሜሪካ እስከ 2013 ነሃሴ ወር ድረስ 5ሺህ ያህል ዜጎቿን በከፍተኛ፣ 18 ሺህ ያህሉን ደግሞ በመለስተኛ ደረጃ በሽብርተኝነት ጠርጥራ የመዘገበች ሲሆን፣ 1ሺህ 200 የራሷን ዜጎች ጨምሮ ሌሎች ተጨማሪ 16 ሺህ የተለያዩ አገራት ዜጎችንም ‘በአየር መንገዶችና በድንበር አካባቢዎች ጥብቅ ፍተሻ ሊደረግባቸው የሚገቡ’ በማለት ስማቸውን መዝግባ ይዛለች፡፡
ግለሰቡ ያወጣቸው እነዚህ አዳዲስ መረጃዎች፣ ስኖውደን መረጃ በማውጣቱ ሰበብ ለእስር እንዳይዳረግ በመስጋት ከአሜሪካ አምልጦ ወደ ሩስያ ከኮበለለ በኋላ በነበረው ጊዜ በአገሪቱ ብሄራዊ የጸረ ሽብርተኝነት ማዕከል  የተዘጋጁ እንደነበሩ መረጋገጡን ጠቁሞ፣ ይህም መረጃዎቹን ያወጣው ሌላ ግለሰብ መሆኑን  የሚያሳይ ነው መባሉን ገልጿል፡፡ የአገሪቱ ባለስልጣናት የአዲሱን መረጃ መንታፊ ማንነት ለማወቅ ጥረት እያደረጉ ሲሆን፣ ግለሰቡ ምናልባትም በሚመለከታቸው የአገሪቱ የደህንነት መረጃ ተቋማት ውስጥ የሚሰራ ሊሆን እንደሚችል መገመቱን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ግለሰቡ ምን ያህል የሚስጥር መረጃዎችን እንዳወጣም ሆነ መረጃዎቹ አፈትልከው መውጣታቸው በአገሪቱ መንግስት ላይ የሚያስከትለውን ጉዳት በተመለከተ የአገሪቱ መንግስት ያለው ነገር ባይኖርም፣ መረጃዎቹ ‘ሚስጥራዊና ለውጭ አገራት መንግስታት ተላልፈው የማይሰጡ መረጃዎች’ በሚል  መለያ በአገሪቱ የደህንነት መረጃ ተመዝግበው እንደነበር ዘገባው ጨምሮ ጠቁሟል፡፡
አዲሱ መንታፊ ያወጣቸው መረጃዎች ስኖውደን ከዚህ በፊት ካወጣቸው የደህንነት መረጃዎች ጋር ሲነጻጸሩ በሚስጥራዊነታቸው አነስተኛ እንደሆኑ ዘገባው ጠቁሞ፣ ስኖውደን ካወጣቸው 1 ነጥብ 7 ሚሊዮን የአገሪቱ የደህንነት መረጃዎች አብዛኞቹ ‘ጥብቅ ሚስጥሮች’ እንደነበሩ አስታውሷል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

የቻይናው የሞባይል ቀፎ አምራች የግል ኩባንያ ዚያኦሚ፣ የእነጋላክሲና አይፎን ዘመን አክትሟል፣ ከአሁን በኋላ ከማንም በላይ ከፍ ብዬ የምታየው የአገሬ ‘የስማርት ፎኖች’ ንጉስ እኔ ነኝ እያለ ነው፡፡
በአገረ ቻይና የስማርት ፎን ገበያ ዋነኛ ተፎካካሪው የነበረውን የደቡብ ኮሪያው ሳምሰንግ በዘንድሮው ሁለተኛ ሩብ አመት ለመጀመሪያ ጊዜ በሽያጭ ያስከነዳውና ተወዳጅነቱ እየጨመረ የመጣው ዚያኦሚ፣ ይህ ስኬቱ በአገሩ ምድር የስማርት ፎን ገበያ መሪነቱን እንዳስጨበጠው ሲኤንኤን ሰሞኑን ከሆንግ ኮንግ ዘግቧል፡፡
ከአራት አመታት በፊት የተመሰረተው የቻይናው ስማርት ፎን አምራች ዚያኦሚ፣ በአገሪቱ ገበያ ያለውን ድርሻ በአጭር ጊዜ ውስጥ በፍጥነት በማሳደግና ባለፈው አመት ተመሳሳይ ጊዜ ከነበረው የገበያ ድርሻ 240 በመቶ ጭማሪ በማድረግ በአሁኑ ወቅት 14 በመቶ ማድረሱ የተነገረ ሲሆን፣ በሩብ አመቱ ለገበያ ያቀረባቸው ስማርት ፎኖች ቁጥርም 15 ሚሊዮን መሆኑ ተዘግቧል፡፡
ዚያኦሚ በተጠቀሰው ጊዜ 97 በመቶ የሚሆነውን ምርቱን ለቻይና ገበያ ያቀረበ ሲሆን፣ የካፒታል አቅሙም ከ10 ቢሊዮን ዶላር በላይ መድረሱ ተነግሯል፡፡  
ሳምሰንግን ጨምሮ ዋነኛ ተፎካካሪዎች የነበሩት ሁዋዌ፣ ሌኖቮና ዩሎንግ በሩብ አመቱ በአማካይ 10 በመቶ የገበያ ድርሻ መያዛቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ዚያኦሚ በቻይና ቀዳሚውን የገበያ ድርሻ ቢይዝም ከአገር ውጭ እምብዛም እንደማይታወቅ አስታውሷል፡፡
ኩባንያው በአገር ውስጥ እያስመዘገበ ያለውን ስኬት በማስፋፋት በአለም አቀፉ የስማርት ፎን ገበያ ተወዳዳሪና መሪ የመሆን ራዕይ ሰንቆ እየሰራ እንደሚገኝ የተገለፀ  ሲሆን፣ ይህን እቅዱን ለማሳካት በሚችልበት መንገድ ዙሪያ ባለፈው አመት ከጎግል ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ጋር የጋራ እንቅስቃሴ መጀመሩም ተዘግቧል፡፡
ዚያኦሚ ወደ አለማቀፉ የስማርት ፎን ገበያ ዘልቆ ለመግባትና ንግስናውን ድንበር ለማሻገር የጀመረውን ጉዞ፣ ምርቶቹን ወደ ሩስያ፣ ኢንዶኔዥያ፣ ሜክሲኮ፣ ታይላንድና ቱርክ በመላክ ለመጀመር እንደተዘጋጀ ታውቋል፡፡
የኩባንያው ስማርት ፎኖች በአሁኑ የቻይና ገበያ በ130 ዶላር እየተሸጡ ሲሆን፣ ዋጋቸው ከአፕል ምርቶች ጋር ሲነጻጸር በአንድ ሶስተኛ ያነሰ እንደሆነ ተነግሯል፡፡


Published in ከአለም ዙሪያ

ትዳር መመስረት የፈለጉ ወንዶች ለመንግሰት ፕሮፖዛል ማቅረብ አለባቸው
የአገሪቱ ወንዶች ከ4 አገራት ሴቶች ጋር መጋባት አይችሉም

ሳኡዲ አረቢያ ከሌሎች አገራት ሴቶች ጋር ትዳር መመስረት ለሚፈልጉ ዜጎቿ ጥብቅ የሆነ የትዳር መመሪያ ማውጣቷንና የአገሪቱ ወንዶች ከአራት አገራት ሴቶች ጋር እንዳይጋቡ መከልከሏን ቢቢሲ ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡
የሳኡዲ መንግስት ያወጣውን የትዳር መመሪያ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ከሌሎች አገራት ሴቶች ጋር ትዳር መመስረት የሚፈልጉ ዜጎች፣ የትዳር ፕሮፖዛልና የሚኖሩበት ከተማ ከንቲባ ፊርማ ያረፈበት የነዋሪነት መታወቂያ ለአገሪቱ ፖሊስ ማቅረብና ማስገምገም ይጠበቅባቸዋል፡፡
የመካ ከተማ ፖሊስ አዛዥ የሆኑት አሳፍ አልቁሪሽ እንዳሉት፣ መንግስት ትዳር ፈላጊዎች የሚያቀርቡለትን ፕሮፖዛል ገምግሞ ፍቃድ ይሰጣል፡፡ አዲሱ መመሪያ እንደሚለው፤ ትዳር ፈላጊው ዕድሜው ከ25 ዓመት በላይ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ ከዚህ ቀደም ትዳር የነበረውና የተፋታ ከሆነ ደግሞ፣ ከሌሎች አገራት ሴቶች ጋር አዲስ ትዳር መመስረት የሚችለው፣ ፍቺው ከተፈጸመ ከከ6 ወራት ጊዜ በኋላ ነው፡፡
“ዘ መካ” የተባለው የአገሪቱ ጋዜጣ ሰሞኑን በጉዳዩ ዙሪያ ያወጣውን ዘገባ ጠቅሶ ቢቢሲ እንደገለጸው፣ ትዳር ፈላጊው የቀድሞ ትዳሩን በህጋዊ ፍቺ ያላፈረሰ ከሆነ፣ አዲስ ትዳር መመስረት የሚችለው በመንግስት ከሚተዳደር ሆስፒታል የቀድሞ ሚስቱ በጸና መታመሟን ወይም መሃን መሆኗን የሚያረጋግጥ አልያም የቀድሞ ሚስቱ አዲስ ትዳር ቢመሰርት እንደማትቃወም የሚገልጽ ማስረጃ ሲያቀርብ ነው፡፡ አዲሱ የሳኡዲ አረቢያ መንግሰት ለአገሪቱ ትዳር ፈላጊ ወንዶች ያወጣው የጋብቻ መመሪያ፣ ወንዶቹ በአገሪቱ ውስጥ በተለያዩ ሙያዎች ተቀጥረው ከሚሰሩ የፓኪስታን፣ ባንግላዴሽ፣ ቻድ እና በርማ ሴቶች ጋር በፍጹም ትዳር መመስረት እንደማይችሉ ጥብቅ እገዳ የሚጥል መሆኑን ዘገባው ያስረዳል፡፡
ሳኡዲ አረቢያ በአለም አቀፍ ደረጃ በርካታ የውጭ አገራት ዜጎች በተለያዩ ስራዎች ተሰማርተው የሚገኙባት ቀዳሚዋ አገር መሆኗን የጠቀሰው ዘገባው፣ ዘጠኝ ሚሊዮን ከሚደርሱት ከእነዚህ የውጭ አገራት ሰራተኞች መካከል 30 በመቶ የሚሆኑት ወይም 500 ሺህ ያህሉ የትዳር እገዳ ከተጣለባቸው አራቱ አገራት የመጡ ሴቶች መሆናቸውን ጨምሮ ገልጧል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

የሩስያ ዜግነት ያላቸው አባላትን የያዘ አለማቀፍ የድረገጽ ሌቦች ቡድን የአሜሪካን ግዙፍ ኩባንያዎች ጨምሮ በዓለም ዙሪያ የሚገኙ ታላላቅ ድርጅቶችን፣ የንግድ ኩባንያዎችንና የግለሰቦችን የድረገጽ መረጃዎችና ፓስ ዎርዶችን (የሚስጥር ቁልፎች) መዝረፉን ቴሌግራፍ ዘገበ፡፡
ሆልድ ሴኪዩሪቲ የተባለውን ተቋም ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ቡድኑ ከ420 ሺህ በላይ በሚሆኑ የኩባንያና የግለሰብ ድረገጾች ላይ የፈጸመው ይህ የስርቆት ተግባር፣ በዘርፉ በአለም ዙሪያ የተፈጸመ ትልቁ የመረጃ ዘረፋ ነው፡፡ ዘራፊዎቹ 500 ሚሊዮን የሚሆኑ የኢሜይል አድራሻዎችን የሚስጥር ቁልፍ በርብረው እንዳገኙ የጠቆመው ዘገባው፣ መሰል ተግባር ከተፈጸመባቸው መካከልም በዓለማችን ከፍተኛ የፋይናንስ አቅም ያላቸው ኩባንያዎች እንደሚገኙበት የሆልድ ሴኪዩሪቲን መስራች አሌክስ ሆልደን መናገራቸውን አስረድቷል፡፡
አስር ያህል አባላትን የያዘው ይህ የዘራፊዎች ቡድን ተቀማጭነቱን ያደረገው፣ ከካዛኪስታንና ከሞንጎሊያ ጋር በሚዋሰነው የሩስያ ደቡብ ማዕከላዊ አካባቢ እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን፣ አባላቱ በሃያዎቹ የዕድሜ ክልል ውስጥ እንደሚገኙ ተነግሯል፡፡
የቡድኑ አባላት የራሳቸውን የኮምፒውተር ፕሮግራም በመፍጠርና የድረገጾችን መረጃ በመስረቅ በሚያገኙዋቸው የሚስጥር ቁልፎች አማካይነት የኩባንያዎችንና የግለሰቦችን የመረጃ ልውውጥና ሚስጥር በእጃቸው እንደሚያስገቡ ተገልጿል፡፡
ኒውዮርክ ታይምስ በበኩሉ፣ቡድኑ የዝርፊያ ስራውን በረቀቀ መንገድ ማከናወን ከጀመረ ጥቂት አመታት እንደሆነው ገልጾ፣ የሚስጥር ቁልፎችን በመዝረፍ የሚያገኛቸውን የኩባንያዎችና የግለሰቦች ሚስጥሮች መደራደሪያ በማድረግ የገንዘብ ምንጭ አድርጎ እንደሚጠቀም ተነግሯል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

በናትናኤል ፋንቱ የተፃፈው “ከነፍስ እስከ ዩኒቨርስ” የተሰኘ መፅሀፍ ባለፈው ሳምንት ለንባብ በቅቷል፡፡ መፅሀፉ በዋናነት በስነ ፈለክ ምርምር፣ በፕላኔቶች፣ በፀሐይና መሰል ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ነው፡፡ “ከነፍስ እስከ ዩኒቨርስ” ስለምንኖርባት ዓለም ምን ያህል እናውቃለን፣ ማወቁስ ለምን አስፈለገ? ስለክዋክብት ማወቅስ ምን ይጠቅማል ለሚሉትና ተያያዥ ጥያቄዎች መጠነኛ መልስ ይሰጣል ተብሏል፡፡ በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች የተከፈለው መፅሀፉ፤ 156 ገፆች ያሉት ሲሆን በ40 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ የመፅሀፉ አዘጋጅ ናትናኤል ፋንቱ ከዚህ ቀደም “የእኔ ስላሴዎች - ህይወት፣ ፍቅርና ሳቅ”፣ “ስለ አረንጓዴ አይኖች”፣ “ሴቶች ለምንድን ነው ወሬ የማያቆሙት?” እና “የአምላክነት ቅምሻ” የተሰኙ መፃህፍትን ማሳተሙ ይታወሳል፡፡

በቀድው የ“አዲስ ነገር” ጋዜጣ አዘጋጅ ጋዜጠኛ ግርማ ተስፋው የተደረሰው “ሰልፍ ሜዳ” የተሰኘ ልብወለድ መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡ የልቦለዱ ማጠንጠኛ ከአብዮት በኋላ በሚያጋጥም የህይወት ፈተና ላይ በተዋቀረ በተለይም የሰው ልጆች በአብዮት ማግስት ለሚኖሩት ህይወት ትርጉም ማጣት፣ ብቸኝነት፣ ድብታና የባዶነት አዘቅት ውስጥ መስጠም በመፅሀፉ እንደ ዋንኛ ጭብጥ ተነስቷል፡፡
240 ገፆች ያሉት ልቦለዱ፤ በሊትማን መፃህፍት አከፋፋይነት የቀረበ ሲሆን በ49 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም “የጠፋችውን ከተማ ሐሰሳ” የተሰኘ የግጥም መድበል ለንባብ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡

በእስክንድር ዋሴ ተደርሶ፣ በሄኖክ ለማ እና በኢያሱ እንዳለ የተዘጋጀው “የብርሃን ፊርማ” የተሰኘ ፊልም የፊታችን ሰኞ ከቀኑ በ11፡00 ሰዓት በብሔራዊ ቴአትር ይመረቃል፡፡ በ“ሱዛና ፒክቸርስ ፊልም ፕሮዳክሽን” የቀረበውና የድራማ ዘውግ ያለው ፊልሙ፣ በዋና ፕሮዲዩሰር እስክንድር ዋሴና በፕሮዲዩሰር ጋዜጠኛ ፅዮን ግርማ እንደተሰራ ታውቋል፡፡ የ1፡30 ርዝመት ያለው ፊልሙ፤ አንዲት በሙዚቃ ፍቅር የተማረከች እናት የህይወትን ውጣ ውረድና መሰናክል ለማለፍ ስትታትር የሚያሳይ ሲሆን ስኬትን፣ እናትነትንና ወጣትነትን የሚያስቃኝ ነው ተብሏል፡፡ በፊልሙ ላይ ሳያት ደምሴ፣ ታደለ ሮባ፣ ማህሌት ሹመቴ፣ ህፃን ማራኪ ዜና፣ ኤልያስ ወሰንየለህና አንዱአለም ተስፋው እንደተሳተፉበት “ሱዛና ፒክቸርስ ፊልም ፕሮዳክሽን” በላከው መግለጫ ጠቁሟል፡፡