አመቱን ሙሉ፣ ኢህአዴግና ተቃዋሚ ፓርቲዎች ስለ አክራሪነት አደጋ እና ስለ ሃይማኖት ነፃነት መላልሰው መላስሰው እየነገሩን ይሄውና ክረምቱ ሊገባደድ ደርሷል። አሳዛኙ ነገር፣ በደፈናው እያድበሰበሱና እያምታቱ ከመናገር ውጭ የአክራሪነትን ምንነት ከነምንጩ፣ እንዲሁም የሃይማኖት ነፃነትን ትርጉም ከነምክንያቱ በግልፅ አፍረጥርጦ የሚናገር አልተገኘም።
የሃይማኖት ነፃነት ማለት፣ እንደየምርጫችን የሃይማኖት እምነቶችን መቀበልና መደገፍ ማለት ብቻ አይደለም። የሃይማኖት እምነቶች አለመቀበልንና መተቸትንም ይጨምራል። እንደየእምነታችን የሃይማኖት ትዕዛዛትን እየተከተልን መፈፀም ማለት ብቻ አይደለም። ትዕዛዛትን እየተቃወሙ አለመፈፀምንም ሁሉ ያካትታል። በአጭሩ የሃይማኖት ነፃነት፣ የሃሳብ ነፃነት ውስጥ የሚጠቃለል አንድ ክፍል ነው።
ታዲያ፣ የሃይማኖት ነፃነት ማለት እምነትን መያዝ ብቻ ሳይሆን ከሃይማኖት ነፃ መሆንንም እንደሚጨምር በግልፅ የተናገረ የፓርቲ መሪ ወይም ተወካይ አጋጥሟችኋል? የሃይማኖት ነፃነት መከበር አለበት የሚባለው፣ ለሃይማኖት ተቋማት፣ ልዩና ከፍተኛ ቦታ በመስጠት አይደለም። ቀድሞ ይሰጣቸው የነበረውን ልዩ ስፍራ በማሳጣት እንደማንኛውም ማህበር፣ የግለሰቦችን ነፃነት ሳይጥሱ የሕግ ተገዢ እንዲሆኑ ለማድረግ ነው የሃይማኖት ነፃነት የሚያስፈልገው። ይህንን እውነት ፊት ለፊት የሚያስረዳ ፖለቲከኛ ወይም ፓርቲስ አይታችኋል? የለም።
አክራሪነት በተፈጥሮው፣ ሃይማኖትን ከማጥበቅ እንደሚነሳ እቅጩን የተናገረ ፖለቲከኛ ሰምታችሁ ታውቃላችሁ? እንዲሁ በደፈናው ለዘብተኛነትን ነው የሚሰብኩት። ለዘብተኛ መሆን ማለት ግን ሌላ ትርጉም የለውም። አንዳንድ የሃይማኖት እምነቶችንና ትዕዛዛትን በዝምታ አይተው እንዳላዩ ማለፍ ማለት ነው። የአክራሪነትና የለዘብተኛነትን ልዩነት በግልፅ ለማሳየት አንድ ምሳሌ ልጥቀስላችሁ።
እርስዎ እና ወንድምዎ ወይም ጓደኛዎ የአንድ ሃይማኖት ተከታይ ናችሁ። ወንድምዎ ወይም ጓደኛዎ፣ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ሃይማኖቱን ቀይሮ እርስዎንም ለመስበክና ለማሳመን ቢሞክር ምን ያደርጋሉ? እስቲ፣ ቁም ነገር ይዞ ከመጣ ልስማው ብለው ያስተናግዱታል? ይከራከሩታል? ወይስ ዞር በልልኝ ይሉታል? ለእንደዚህ አይነት አጋጣሚ የሚሆን ነገር በሃይማኖት መፅሃፍዎ ውስጥ የሰፈረ ትዕዛዝ ቢኖርስ? እስቲ ይህንን እንመልከት፡
“የእናትህ ልጅ ወንድምህ ወይም ወንድ ልጅህ፣ ሴት ልጅህ ወይም ሚስትህ፣ ወይም እንደ ነፍስህ ያለ ወዳጅህ፣ [በዙሪያህ ከቅርብ የሚገኙ ሕዝቦች ወይም ከምድር ዳር ከሩቅ የሚኖሩ ሕዝቦች የሚከተሉትን ሃይማኖት አምጥቶ፣ አማልክቶቻቸውን እናምልክ] ብሎ ቢያስትህ፣ እሺ አትበለው። አትስማው፤ ዓይንህም አይራራለት። አትማረው፣ አትሸሽገው። ይልቁንስ ግደለው። እርሱን ለመግደል የአንተ እጅ ይቅደም፣ ከዚያም በኋላ የሕዝቡ ሁሉ እጅ ይውረድበት። ከአምላክህ ሊያርቅህ ወድዶአልና እስኪሞት ድረስ በድንጋይ ውገረው። ሕዝቡም ሁሉ ሰምተው ይፈራሉ፣ እንዲህም ያለ ክፉ ሥራ እንደ ገና በአንተ መካከል አያደርጉም።
… ሌሎችን አማልክት እናምልክ ብለው የከተማቸውን ሰዎች አሳቱ ሲሉ ወሬ ብትሰማ፣ … ይህም ክፉ ነገር እንደ ተደረገ እርግጥ ሆኖ ቢገኝ፣ የዚያችን ከተማ ሰዎች በሰይፍ ስለት ፈጽሞ ትመታቸዋለህ። ከተማይቱን፣ በእርስዋም ያለውን ሁሉ፣ እንስሳውንም በሰይፍ ስለት ታጠፋቸዋለህ። …ከተማይቱንም ዕቃዋንም ሁሉ ለአምላክህ በእሳት ታቃጥላለህ፤ ለዘላለምም ወና ትሆናለች።”
የሃይማኖታዊ እምነት ሰባኪዎች፣ እነዚህን ትዕዛዛት በበርካታ አስገራሚ መንገዶች ሊተነትኗቸውና ሊተረጉሟቸው እንደሚችሉ አያጠራጥርም። በቀጥታ አንብበን የምንገነዘበው ጭብጥ ግን ብዙም የሚሻማ አይደለም። ካንተ አካባቢና ከተማ ውጭ፣ በሩቅና በቅርብ የሚኖሩ ሰዎች በሌላ ሃይማኖት ሌላ አምላክ ያመልኩ ይሆናል።
በቤተሰብህ፣ በአካባቢህና በከተማህ ውስጥ፣ ያንተው አይነት ሃይማኖት ሲከተሉ የነበሩ ሰዎች ሃይማኖታቸውን ሲቀይሩ ወይም ሲሰብኩ ግን፣ ምህረት የማይደረግለት ጥፋት ነው። (ዋናው ትኩረት፣ የሌላ ሃይማኖት ተከታዮች ላይ አይደለም)
ሃይማኖታቸውን ቀይረው የሚሰብኩ ሰዎችን ትገድላለህ። ስብከቱን ሰምተው ሃይማኖታቸውን የቀየሩትንም ሰዎች፣ በከተማዋ ያሉትን እንስሳት ጭምር ትጨፈጭፋለህ። (ዋናው ትኩረት፣ ያንተ አይነት ሃይማኖት የሚከተሉ ሰዎች ላይ ነው)
እንግዲህ ከላይ የተጠቀሱትን ትዕዛዛት ከምር ተቀብሎ ቀጥተኛ ትርጉማቸውን የሚከተልና የሚሰብክ፣ ከምር ተግባራዊ መደረግ አለባቸው ብሎ የሚያምንና የሚንቀሳቀስ ሰው ነው አክራሪ ማለት።
ሌሎቻችንስ ምን እናደርጋለን? ከአክራሪዎች የተለየ አማራጭ እናፈላልጋለና። ደግሞም፣ በርካታ የተለያዩ መንገዶች አሉ። “እነዚያ ትዕዛዛት፣ በቀጥታ ከሚያስተላልፉት ግልፅ መልዕክት የተለየ ሚስጥራዊ ትርጉምና ድብቅ መልዕክት ይኖራቸው ይሆናል” ብለን ማለፍ እንችላለን። አንድ ዘዴ ነው። ቀጥተኛውን ትርጉም ውድቅ የሚያደርጉ ተቃራኒ ሃይማኖታዊ ትዕዛዛትንና ጥቅሶችን መዘርዘርም ሌላ ዘዴ ነው። አንዱን ጥቅስ በሌላ ጥቅስ እናለዝበዋለን።
ይሄ ሁሉ አላስኬድ ቢለን እንኳ፣ የትዕዛዛቱን ቀጥተኛ ትርጉም አይተን እንዳላየን ችላ የምንል እንኖራለን። ለዘብተኛነት ይሄው ነው። ሃይማኖታዊውን እምነትና ትዕዛዛቱን በጥቅሉ እንቀበላለን ብንልም፣ የተለያዩ ዘዴዎችን በመጠቀም አንዳንዶቹን እምነቶችና ትዕዛዛት ቸል በማለት በሰላም ኑሯችንን ለመቀጠል እንሞክራለን። ችግር የሚመጣው፣ አክራሪዎች ሲያፋጥጡን ነው - ለዚያውም በሦስት ተከታታይ ማፋጠጫ ፈተናዎች።

አንደኛ፡ አማኝ ነህ
“አማኝ ሃይማኖተኛ ነኝ እስካልክ ድረስ፣ ሁሉንም እምነቶች መቀበልና ሁሉንም ትዕዛዛት ተግባራዊ ማድረግ የሃይማኖት ግዴታችሁ ነው” ለሚሉን አክራሪዎች፣ ምላሻችን ምን ይሆናል? ሰው መግደልና ከተማውን ሙሉ ህፃን ከአዋቂ ሳልል ማቃጠል አእምሮዬ አይቀበለውም ማለት እንችላለን። ነገር ግን፣ በዚህ መከራከሪያ መቀጠል የምንችለው፣ ከእምነት በፊት ለአእምሮ ቅድሚያ የምንሰጥ ከሆነ ብቻ ነው።

ሁለተኛ፡ አገልጋይ ነህ
“ደግሞስ፣ ስለሌሎች ሰዎች ሃይማኖት ምን አገባኝ? እምነታቸውን ቢለውጡ ወይም ባይለውጡ የራሳቸው ምርጫ ነው” የሚል ሌላ መከራከሪያ ብናመጣ ያዋጣናል። የኔ አላማ በራሴ ጥረት ኑሮዬን ማሻሻልና ከቀና ሰዎች ጋር መገበያየት እንጂ፣ የሌሎች ሰዎችን ሕይወትና ኑሮ ለመምራት መሞከር አይደለም ብለን እንሞግታቸው። ግን እነሱም፣ የራሳችንን እምነት በመጠቀም ማጥመጃ ያዘጋጃሉ። “የሃይማኖት ትዕዛዛትን የምትፈፅም የፈጣሪ አገልጋይ እንደሆንክ ታምናለህ? ወይስ ለራስህ አለማዊ የግል አላማ ቅድሚያ ትሰጣለህ?” ብለው ያፋጥጡናል።
በእርግጥ፣ ሰባኪዎች “ፈጣሪን ለማገልገል ትዕዛዛቱን ፈፅም” ብለው ሲነግሩን፣ “የፈጣሪ ትዕዛዛት ወዳንተ የሚደርሱት በኔ በኩል ነው፤ አንተ በታዛዥነት ፈፅም” ማለታቸው እንደሆነ ይገባን ይሆናል። የፈጣሪ ቃል አቀባይ ሆነው መቅረባቸውም ላይዋጥልን ይችላል። ነገር ግን፣ ይሄ ማምለጫ አይሆነንም። “ለራሱ የግል አላማ ቅድሚያ የማይሰጥ አማኝ፣ ፈጣሪን ለማገልገል ትዕዛዛቱን ይፈፅማል” በማለት ሲያፋጥጡን፣ የሚያጠግብ ምላሽ ከሌለን እግራቸው ስር መንበርከካችን አይቀርም። “የፈጣሪን ትዕዛዛት መፈፀም ግዴታ ነው” ብለው ይጨምሩበታል።

ሦስተኛ፡ ግዴታ አለብህ
“ከራስ ጥቅም በፊት፣ ለአገር ልማትና ለሕዝብ ጥቅም ቅድሚያ መስጠት ግዴታ ነው” እንደሚባለው አይነት ነው። ብዙ ሰው፣ “የአገር አገልጋይ፣ የሕዝብ ባሪያ ነህ” ተብሎ ሲነገረው፣ ለመቃወም አይሞክርም፤ ይስማማል እንጂ።
በርካታ የዩኒቨርስቲ ተመራቂዎች፣ የወደፊት አላማቸው ምን እንደሆነ ሲጠየቁ፣ “አገሪቱን ለማልማት፣ ሕዝቡ የሚጠብቅብኝን ሁሉ ለመስራትና ለመወጣት ዝግጁ ነኝ” ብለው ሲናገሩ ሰምታችሁ ይሆናል። ለምን? የግል አላማ መያዝ እንደ ወንጀል አልያም እንደ ነውር ይቆጠራላ። እንዲህ አይነቱ “ሕዝባዊ ስሜትን” የሚያመልክ አስተሳሰብ ነው፣ ከ50 አመታት በላይ በአገራችን ሰፍኖ የቆየው።
በእርግጥ፣ “ማንም ሰው ማንንም የማገልገል ግዴታ የለበትም” የሚል በሳይንሳዊ እውቀት ላይ የተመሰረተ አስተሳሰብ በማምጣት፣ የሃይማኖት አክራሪዎችንና ሕዝባዊ ካድሬዎችን መከላከል ይቻላል። ከ230 አመታት በፊት ለአሜሪካ ምስረታ የተዘጋጀው የነፃነት መግለጫ ጥሩ ምሳሌ ነው።
የመንግስት ሃላፊነትና ስራ የእያንዳንዱን ሰው መብት ማስከበር እንደሆነ መግለጫው በአፅንኦት ያስገነዝብና፣ ከእነዚህ መብቶች መካከልም፣ የሕይወት መብት፣ የነፃነት መብትና ደስታን የመሻት መብት ይጠቀሳሉ ይላል። የቃላት አመራረጣቸው ድንቅ ነው። ሶስቱንም መብቶች በየተራ እንያቸው።
ከሁሉም በፊት፣ የአንድ ሰው ሕይወት የማንም ንብረት አይደለም - የራሱ የሰውዬው እንጂ። የራሱን ኑሮ የሚመራው ደግሞ በራሱ ነፃ አእምሮና ምርጫ እንጂ በሌላ ሰው ትዕዛዝ አይደለም። ይሄ ነው የነፃነት መብት። የእያንዳንዱ ሰው በጥረቱ የራሱን ሕይወት የማሻሻልና ደስታን የመቀዳጀት አላማውን እንዳያሳካ የሚያግደው ሃይል መኖር የለበትም - ማንንም የማገልገል ግዴታ የለበትምና። የራሱን ደስታ በራሱ ጥረቱ የመሻት መብት አለው። ለሳይንሳዊ እውቀት ከሁሉም የላቀ ክብር የሰጡ የአሜሪካ መስራቾች፣ በዚህ መንገድ ነው ስልጡን የፖለቲካ ስርዓትን የገነቡት። የሃይማኖት አክራሪነትን ለማሸነፍ የቻሉትም በዚሁ ምክንያት ነው። እኛም ሳይንሳዊ እውቀት የበላይነት እንዲይዝ በማድረግ አክራሪነትን መከላከል እንችላለን።
“አማኝ ሃይማኖተኛ ነኝ እያልክ፤ እንዴት ማንንም የማገልገል ግዴታ የለብኝም ትላለህ?” ብለው አክራሪዎች ሲያፋጥጡን የምንሰጣቸው ምላሽ ላይ ነው ቁልፉ ያለው።
የአክራሪዎች ማጥመጃ ግን ይሄ ብቻ አይደለም። በሃይማኖቶች መካከል ፉክክርና ተቀናቃኝነት በመፍጠር፣ ከዚያም አልፈው ቅራኔና ግጭት በመዝራት፣ “የኛ ወኪል፤ የሃይማኖታችን ጠበቃ” አድርገን በራሳችን ፈቃድ ዘውድ እንድንጭንላቸው ያደርጋሉ። ከዚያ በኋላማ ስለታቸውን ወደኛው ያዞሩብናል።
ከላይ የተጠቀሰው ሃይማኖታዊ ትዕዛዝ በደንብ አይታችሁት እንደሆነ፣ ዋናው ትኩረቱና ፀቡ፣ ሌላ ሃይማኖትን ከሚከተሉ ሰዎች ጋር አይደለም። የሃይማኖት አክራሪ ዋነኛ ኢላማም፣ ሌላ ሃይማኖት በሚከተሉ ሰዎች ላይ ያነጣጠረ አይደለም። እንደሱ አይነት ሃይማኖት የሚከተሉ ሰዎችን በጅራፍ እየዠለጠ፣ በብረጥ እየቀጠቀጠ ሰጥ ለጥ አድርጎ መቆጣጠርን፣ እምቢ ያለውን ደግሞ እያቃጠለና እያረደ መጨፍጨፍን ነው የሚፈልገው።
በእርግጥ፣ ይህ ሁሉ የአክራሪ ጉድ በግላጭ ከመታየቱ በፊት፣ በቅድሚያ “የሃይማኖታችን ተቆርቋሪ!” ብለን በፈቃደኝነት እንድንሾመው በርካታ ዘዴዎችን መጠቀሙ አይቀርም። በየዘመኑና በየሃይማኖቱ የተፈጠሩ አክራሪዎችን በምሳሌነት እንጥቀስ።

የአይሁድ አክራሪ፣ አይሁዶችን ያሰቃየ
ከላይ የተጠቀሰው ሃይማኖታዊ ትዕዛዝ፣ ከኦሪት ዘዳግም በቁንፅል የተወሰደ ጥቅስ ቢሆንም፣ በተለያዩ ሃይማኖቶች ውስጥ የሚፈለፈሉ አክራሪዎች ተመሳሳይ ጥቅሶችን የታጠቁ ናቸው። ከሁለት ሺ አመታት በፊት፣ በእስራኤል አገር ገናና ለመሆን የቻለ አክራሪ የአይሁድ ቡድን፣ ከሃይማኖት መፅሃፍ ውስጥ እልፍ ትዕዛዛትን እየጠቀሰ ነው አማኞችን ሲያሰቃይ የነበረው። “ያንን ትዕዛዝ አፈረስክ፣ ይሄን ትዕዛዝ አጎደልክ” እያለ ይገርፋል፣ በድንጋይ ይወግራል፣ ይገድላል። “ገደል ውስጥ የገባውን በሬ አውጥተህ ያዳንከው በሰንበት እለት ነው” የሚለው ውንጀላ በጊዜው ተራ ውንጀላ አልነበረም። “በሰንበት እለት አንዳችም ነገር እንዳትሰራ ከፈጣሪ የተሰጠህን ትዕዛዝ አፍርሰሃል” ተብለህ ይፈረድብሃል።
ታዲያ አክራሪው ቡድን፣ እንዲህ የአገሬውን አማኝ ከማሰቃየቱ በፊት፣ በአማኞች ዘንድ ገናናነትን ለመቀዳጀት ዘዴ ማበጀት ነበረበት። ተሳክቶለታልም። በወቅቱ “እስራኤልን በቅኝ ግዛት ተቆጣጥሮ ሃይማኖታችንን ያረከሰውን የሮም ወራሪ ሃይል እንዋጋለን” በማለት የሃይማኖት ተቆርቋሪነት ዝናና ማዕረግ ከአማኞች ዘንድ አግኝቷል። ከዚያ በኋላ ነው፣ አክራሪው ቡድን ወደ ዋናው ትኩረቱ በመዞር፣ የአገሬውን አይሁዶች ቁምስቅላቸውን ያሳያቸው የጀመረው።

ግማሽ ያህሉን አማኝ የጨረሰ የክርስትና አክራሪ
ለሺ አመታት በተለያየ መልክ የተፈለፈሉ የክርስትና አክራሪዎችም እንዲሁ፣ ተቻኩለው በቀጥታ ክርስትያኖችን የማሰቃየት ዘመቻ አልጀመሩም። በቅድሚያ “የክርስትና ተቆርቋሪ” የሚል ማዕረግ ለማግኘት ተሯሩጠዋል። የሮምና የግሪክ እምነቶች ላይ ጥቃት ለመሰንዘር፣ ከአይሁድ እና ከእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ጋር ግጭት ለመፍጠር ብዙ ደክመዋል።
“የክርስትና ተቆርቋሪነታቸውን” ካስመሰከሩ በኋላ ግን፣ ወደ ዋና አላማቸው በመዞር፣ ካቶሊክ፣ ፕሮቴስታንት፣ ኦርቶዶክስ፣ መናፍቅ … ምናምን እያሉ በእሳት ማቃጠል፣ በሰይፍ መቅላት፣ በድንጋይ መውገር… ያልተፈፀመ የጭፍጨፋ አይነት የለም። ቀላል እንዳይመስላችሁ። በእያንዳንዱ ሃይማኖታዊ ዘመቻና ጦርነት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች አልቀዋል።
በ17ኛው ክፍለ ዘመን መግቢያ ላይ ወደ 20 ሚሊዮን ገደማ የነበረው የጀርመን ህዝብ ቁጥር፣ በጥቂት አመታት ውስጥ ወደ 10 ሚሊዮን የወረደው፣ የክርስትና አክራሪዎች በክርስትያኖች ላይ በለኮሱትና ባካሄዱት ሃይማኖታዊ ዘመቻና ጦርነት ነው። ፈረንሳይ ውስጥ በ16ኛው ክፍለዘመን ማብቂ ላይ ለ30 አመታት በተካሄደ ሃይማኖታዊ ግጭትና ጦርነት 3 ሚሊዮን ሰዎች ተቀጥፈዋል። በክርስትና አክራሪዎች ነው፣ ክርስትያኖች ያለቁት።

በእስልምና አክራሪዎች ያለቁ ሙስሊሞች
በየዘመኑና በየአገሩ የተፈለፈሉ የእስልምና አክራሪዎችም እንዲሁ፣ ከክርስትና ወይም ከአይሁድ እምነት ተከታዮች ጋር በመጋጨት የሃይማኖት ተቆርቋሪነታቸውን ካሳወጁ በኋላ፣ እንደተለመደው ሙስሊሙን ነው መጨፍጨፍ የቀጠሉት። ባለፉት አመታት ኢራቅ ውስጥ በአክራሪዎች የተፈፀመውን የሽብር ዘመቻ ማየት ይቻላል። ፀረ አሜሪካ ፕሮፓጋንዳ በመንዛት በኢራቅ ውስጥ ገናናነትን ለማግኘት ዘመቻ ካካሄዱ በኋላ ነው፣ ኢራቃውያን ላይ ሰይፋቸውን የመዘዙት። ሺዓ ትክክለኛ እስልምና አይደለም ብለው ገደሉ። ከዚያም ለዘብተኛ ሱኒዎች ከሃዲዎች ናቸው ብለው ጭፍጨፉውን ገፉበት።
የጥንቶቹ አክራሪዎችም በተመሳሳይ መንገድ፣ ሺዓ፣ ሱኒ፣ ሱፊ … እያሉ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሙስሊሞችን ጨርሰዋል። በ14ኛው ክፍለዘመን መገባደጃ ላይ ቲሙር ወይም ቲመርሌን ተብሎ የሚታወቀውና ራሱን እስላማዊ ሰይፍ ብሎ የሚጠራው ገዢ ባካሄዳቸው ወረራዎች ከ10 ሚሊዮን በላይ ሰዎች አልቀዋል። በጦርነት የተቆጣጠራት አንዲት ከተማ ውስጥ፣ ለመቀጣጫ ብሎ ከመቶ ሺ በላይ ሰዎችን አንገታቸውን ቆርጦ፣ 50 የጭንቅላት ክምር ፒራሚዶችን ሰርቷል። በአክራሪ ሙስሊሞች ጭካኔ ነው፣ ብዙ ሙስሊሞች የተጨፈጨፉት።
ሰዎች አትሳሳቱ! የሃይማኖት አክራሪነት ብዙዎቻችን እንደምናስበው ቀላል አደጋ አይደለም። ባለፉት መቶ ወይም ሁለት መቶ አመታት፣ በአለማችን ውስጥ የአክራሪነት አደጋና እልቂት እንደ ጥንቱ ገንኖ ሳይወጣ የቆየው፣ ሃይማኖታዊ እምነት የበላይነቱን አጥቶ ስለቆየ ነው። የመቶ አመታት ታሪክ ውስጥ ከቁጥጥር ውጭ የሆነ እንደሰደድ እሳት የሚንሰራፋ የአክራሪነት አደጋ ስላላየን፣ ዛሬም ከቁጥጥር ውጭ አይሆንም ብለን የምንፅናና ከሆነ፣ ተሳስተናል።
የሃይማኖት አክራሪነትና እልቂቱ የረገበው፣ በ17ኛውና ከዚያም በ18ኛው ክፍለ ዘመን፣ በሃይማኖታዊ እምነት ፋንታ ሳይንሳዊ እውቀት የበላይነት እየያዘ ስለመጣ ነው። “የብርሃነ እውቀት ዘመን” ወይም “የአእምሮ ዘመን” ተብሎ በሚታወቀው በዚያ ዘመን ነው፣ የግለሰብ ነፃነት ክብር አግኝቶ ስልጡን የፖለቲካ ስርዓት ስር መስደድ የጀመረው።
የአሜሪካ ህገመንግስትን ተከትሎ፣ በየአገሩ ለግለሰብ ነፃነት ዋጋ የሚሰጡ ጭላንጭሎች ብቅ ብቅ እያሉና ህገመንግስቶች እየተበራከቱ፣ ኢትዮጵያ ውስጥም የነፃነት ጠብታዎች መታየት እየጀመሩ ነበር። ለግለሰብ የንብረት ባለቤትነት እውቅና የሚሰጥ፣ የግለሰቦች የደብዳቤ ልውውጥ እንዲሁም መኖሪያ ቤትን ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ መደፈር እንደሌለበት የሚገልፅ የአገራችን ህገመንግስት የፀደቀው በ1923 ዓ.ም ነው። ይህችው ትንሽዬ ጅምር እየተስፋፋች አልሄደችም።
ሳንይሳዊ እውቀት ቀደም ሲል በሃይማኖታዊ እምነት ምትክ የበላይነትን እንደተቆጣጠረው ሁሉ፣ በ20ኛ ክፍለ ዘመን ደግሞ የሶሻሊዝምና የፋሺዝም ሕዝባዊ መፈክር የበላይነት አግኝቶ ስለነበር፣ ሃይማኖታዊ እምነት እንደድሮው የመግነን እድል ሳያገኝ ቆይቷል። ዛሬ ግን በሩ ተከፍቶለታል።
የግለሰብ ነፃነት የሚከበርበት ስልጡን የካፒታሊዝም ስርዓት እየተጠናከረ የሚጓዝበት ዘመን ላይ አይደለንም - ሳይንሳዊ እውቀት የበላይነቱን አጥቷል። በአገርና በሕዝብ፣ በጭቁኖችና በብሄር ብሄረሰብ ስም፣ የሶሻሊዝምና የፋሺዝም አምባገነንነት እየተስፋፋ የሚሄድበት ዘመን ላይም አይደለንም - “ሕዝባዊ መፈክር” የበላይነቱን አጥቷል። የአስተሳሰብ ኦና በመፈጠሩም ነው፣ ሃይማኖታዊ እምነት ቦታውን ለመሙላትና የበላይነቱን ለመቆጣጠር እየሞከረ ያለው።
ይህን የአክራሪነት ማዕበል በቀላሉ መመለስ የሚቻለው፣ ሳይንሳዊ እውቀት የበላይነት እንዲይዝ በማድረግ ነው። ነገር ግን ይህንን እያደረግን አይደለም። አስፈሪነቱም እዚህ ላይ ነው። አክራሪዎች ሃይማኖታዊ እምነትን ታጥቀዋል። ሌሎቻችን ግን፣ ኢህአዴግና ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ጨምሮ፣ በተበረዘና በተከለሰ፣ በተቀየጠና በተዘበራረቀ ቁርጥራጭ አስተሳሰብ ግራ ከመጋባትና ከመደናበር ውጭ የጠራ አስተሳሰብ አልታጠቅንም። ፓርቲዎቹ ስለ አክራሪነትና ስለ ሃይማኖት ነፃነት በተደጋጋሚ እያወሩ፣ ነገርን ከማድበስበስ በስተቀር አንዳች የሚጨበጥ ቁም ነገር ጠብ ሲላቸው የማናየውም በዚህ ምክንያት ነው።

 

Saturday, 31 August 2013 11:59

‘የተሻለ ጊዜ’ መናፈቅ…

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
እንኳን ለዋዜማ ሰሞን አደረሳችሁማ! መቼም ‘የተሻለ ጊዜ’ የሚሉትን ማየት ከህልምነት ወደ ቅዠትነት እየተለወጠ ያለ የሚያስመስሉ ነገሮች ቢበዙብንም፣ ካለፉት ብዙ ዓመታት ይልቅ ባለፈው አንድ ዓመት ብቻ ‘መንገድ እየሳቱ’ የሄዱ ነገሮች እየበዙብን ቢሆኑም፣ “ሆዴ፣ አካላቴ…” ከማለት ይልቅ “አካኪ ዘራፍ…” የምንል ሰዎች እየበዛን ብንሄድም፣ ይቺን ‘የፈረደባት’ አገር እንደ ግል ‘ርስተ ጉልታችን’ የፈልግነውን ልናደርጋት ‘ሊቼንሳ ያለን’ የሚመስለን ቁጥራችን ቢጨምርም ደግ መመኘት ክፋት ስለሌለው …መጪውን ጊዜ ‘የተሻለ’ ያድርግልንማ!
የአምናን ቀን ረገምኩት ለአፌ ለከት የለው
የዘንድሮው መጣ እጅ እግር የሌለው፡፡
ከሚል አልላቀቅ ያለን እንጉርጉሮ የሚያላቅቀን ‘የተሻለ ጊዜ’ ይሁንልንማ!
የዘንድሮ ዓመት መለስ ብላችሁ ስታዩት…አለ አይደል…ከሚያስደስቱ ነገሮች ይልቅ የሚያስከፉት አልበዙባችሁም! የማይሰበሩ በሚመስሉ መስታወቶች የሚብለጨለጩ ህንጻዎች ከተማዋን እየወረሯት…‘ተሰባሪ’ ሰዎች እየበዙ ያሉበት ዘመን በእርግጥም ያሳስባል፡፡
ስሙኝማ…ካለፉት ጥቂት ሳምንታት ከተማ ውስጥ ከገጠር የመጡ የሚመስሉ የሚለምኑ ሰዎች አልበዙባችሁም! እንዴት ነው እንዲህ ሊሆን የቻለው! ህጻናቶቻቸውን ሰብስበው ወደ አዲስ አበባ በዚህ አይነት ብዛት ለመፍለስ ያስገደዳቸው ምን እንደሆነ የማይነገረንሳ! አሀ…ልክ ነዋ ይሄ “ሁለት ዲጂት…” ምናምን የሚባለው ነገር እነሱን አያካትትም? ለነገሩ በቀደም “የምትበልጡት ኒጀርን ብቻ ነው…” ብለው አወጡብን አይደል!)
እናላችሁ…አንዱ ዓመት አልፎ ሌላው ሊተካ ነው፡፡ ስሙኝማ…ዘንድሮ በአቆጣጠሩ አንድ ዓመት ባለፈ ቁጥር በአኗኗር ደግሞ ወደ አራት ዓመት ገደማ ይሆናል፡፡ ልክ ነዋ…ይኸው ስንቱ ‘ወጣት የነብር ጣት’ አለጊዜው እየገረጀፈ አይደል! አንዱ ወጣት ምን አለ መሰላችሁ… “አባቴ የጥንቱን እያስታወሰ ድሮ በግ በአምስት ብር ይገዛ ነበር ምናምን ይለኝ ነበር፡፡ ዘንድሮ ደግሞ እኔ ከሁለት ወር በፊት እኮ አንድ ቅቅል ሃያ አራት ብር ነበር፣ አሁን አርባ ብር ሆኗል፡፡”
እናማ…‘የድሮ ጊዜ’ ስፋት እየጠበበ በአሥርት ዓመታት ሳይሆን… በ‘ወራት’ መቆጠር እየጀመረ ነው፡፡ “እንኳን ከዘመን ዘመን አሸጋገረህ” ስንባባል…አለ አይደል…ልክ “እንኳን በአንድ ዓመት የአራት ዓመት ዕድሜ ጨመርክ…“ አይነት እየሆነ ነው፡፡
ከዚህ በፊት ያወራናትን ልድገማትማ…አንድ ወዳጄን ጓደኛው ‘ዕድሜ ጠገብ’ መሆኑን ሲነግረው ምን አለው መሰላችሁ…“አንተ እኮ ሀሊ ኮሜትን ሁለቴ አይተህ ሦስተኛ ጊዜ እየጠበቅሀት ነው፡፡” ምን መሰላችሁ…ሀሊ ኮሜት የምትመጣው በየስንት ጊዜ መሰላችሁ…በየስድሳ ዓመቷ!
ስሙኝማ…የጊዜን ነገር ካነሳን አይቀር በጣም ትልቅ የሆነ በሽታ ምን መሰላችሁ…የመጣንበትን ‘ሆነ ብሎ’ መርሳት! በተለይ በሆነ ነገር ‘ስኬት አገኘ/ኘች’ የሚባሉ ሰዎች የመጡበትን መንገድ ሲጠየቁ ቅልጥ ያለ ኮረኮንች የነበረውን በ‘ሬድ ካርፔት’ ያነጥፉታል፡፡
ስሙኝማ…በፊት እኮ ሀብታም የሆኑ ሰዎች ሲጠየቁ…አለ አይደል…“መጀመሪያ ቄጤማ እሸጥ ነበር…” “እህል በረንዳ የጉልበት ሥራ እሠራ ነበር…” ምናምን ብለው እቅጯን ያገሩ ነበር፡፡
የዘንድሮ ‘ባለገንዘብ’ ግን ልክ ሲወለድ ሰባት ቁጥሮች ያሉት የባንክ ደብተር በቀኝ እጁ ይዞ የወጣ ነው የሚመስለው፡፡ እናማ… በዘንድሮ የ‘ገንዘብ ስኬታቸው’ ያለፈ ታሪካቸውን ‘አፈር ድሜ የሚያገቡ’ መአት ናቸው፡፡
እናላችሁ…የመጣንበትን የምንረሳ ሰዎች በዝተናል፡፡
ዘንድሮ መቼም በቀጥታም በተዘዋዋሪም ‘ቦተሊከኛ’ ያልሆንን ጥቂት ነን፡፡ እናላችሁ…ሁላችንም… ምን አለፋችሁ…ዓለም በሙሉ ‘የሚድንበት ቅዱስ ቃል’ ጋር ያለ ነው የሚመስለን፡፡ ታዲያላችሁ…
የዘንድሮ ‘ቦተሊከኞችን’… “ለመሆኑ ፖለቲካ ውስጥ እንዴት ገቡ?” ሲባል “ይገርምሀል፣ ከልጅነቴ ጀምሮ ድሀ ሲበደል ማየት አልወድም ነበር…” ምናምን ነገር ይላል፡፡
እንትናዬ “አስተዳደግሽ እንዴት ነው?” ስትባል ምን ትል መሰላችሁ…
“ውይ! ምን ልበልህ፣ ብቻ አይደለም በዓል መጥቶ አዲስ ልብስ የሚገዛልኝ በየወሩ ነበር፡፡ ነገርዬው እኮ…አለ አይደል…የጎረቤት ሰዎች እኮ አባቷን.. “አቶ…. ኸረ እባክህ ይቺ ልጅ ሦስት ዓመት ሙሉ አንዲት ጨርቅ ሳትለውጥ…እግዜሐሩስ ምን ይላል!” ይሉ ነበር፡፡
ለከርሞ መጽሐፍ ማንበብ…
“ይገርምሀል…በልጅነቴ መፅሐፍ በጣም አነብ ስለነበር እንዳላብድ ፈርተው መፅሐፎች ይደብቁብኝ ነበር…” አይነት ጉራ ሞልቶላችኋል፡፡ ምን መሰላችሁ… እዚህ አገር ጉራ ሲነዛ እስከ ጥግ ነው የሚኬደው! (ከብዙ ጊዜ በፊት አንድ ትንሽ አእምሮ ችግር ስለገጠመው ሲወራ ምን ይባል ነበር መሰላችሁ…“ዲክሺነሪ መሸምደድ ጀምሮ ደብልዩ ላይ ሲደርስ ሳተ…” ይባል ነበር፡፡
ደግሞላችሁ ሌላው አለ…መጀመሪያ ላይ “እዚህ አገር ምን ሰዓሊ አለና ነው!” ምናምን ብሎ ለታሪኩ መግቢያ ምናምን ይሠራል፡፡ ከዚያ ዋናው ታሪክ ይመጣል… “የሚገርምህ ነገር የእንቁጣጣሽ አበባ ስስል አጎቴ ‘ይሄ ልጅ ሲያድግ ቫን ጎህ ይሆናል’ ይል ነበር፡፡” አጎትዬው እኮ፣ አይደለም ቫን ጎህን ሊያውቅ፣ ዓለም ላይ ከሀበሾች በስተቀር ያሉ ህዝቦች ጣልያኖችና ደርቡሾች ብቻ የሚመስሉት አይነት ነው! እና የመጡበትን ‘ሆነ ብሎ የሚያስረሳ’ አብሾን የሚያጠፋልን የተሻለ ጊዜ ያምጣልንማ!
እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ይቺን ስሙኝማ…ሁለት ወዳጆች አውቶብስ ይሳፈራሉ፡፡ እናማ… ትርፍ ወንበር የነበረችው አንድ ብቻ ስለነበረች ‘አንተ ተቀመጥ… አንተ’ ምናምን እያሉ ይግደረደራሉ፡፡ አንደኛው ምን ይላል… “ግዴለም በዕድሜም በለጥ ስለምትለኝ አንተ ተቀመጥ” ይለዋል፡፡ ጓደኛው ምን ቢለው ጥሩ ነው…ተው እባክህ አንተ እኮ የአንዱን ባቡር አይተህ የሁለተኛውንም ባቡር ልታይ ነው፡፡”
እናማ… “ሦስት መንግሥት አይቷል…” እንደሚባለው ‘ሁለት ባቡር ማየት’ም የዕድሜ ባለጸጋነት ምልክት ሊሆን ነው፡፡
አንደ ወዳጄ ታክሲ ላይ ያየትን ጥቅስ ምን ይል መሰላችሁ…“ታሪኩን የማያውቅ ሰውና ስፖክዮ የሌለው መኪና አንድ ናቸው፡፡” አሪፍ አይደል!
ታዲያላችሁ…ልክ ሰው የሌለበት ዓለም ላይ የኖርን ይመስል… ለራሳችን የምንፈጥራቸው ልብ ወለድ ታሪኮችን ስንናገር…‘ምላሳችንን ያዝም’ አያደርገንም፡፡
እናማ ለራስ የልብ ወለድ ታሪክ መጻፍን የሚያስቀር ‘የተሻለ ጊዜ’ ያምጣልንማ!
ታዲያላችሁ…ቤተሰብን የሚያስተሳስሩ ክሮች እየላሉ፣ ወላጆች የወላጅነት ግዴታቸውን እየረሱ ሲሄዱ ማየት “የእውነት የተሻለ ቀን መቼ ነው የሚመጣው?” የማያሰኝሳ! ይቺን የጥንት ግጥም ስሙልኝማ…
በበጋ እረስ ቢሉት ፀሀዩን ፈራና
በሐምሌ እረስ ቢሉት ዝናቡን ፈራና
ልጁ እንጀራ ቢለው በጅብ አስፈራራ
አዎ፣ የዚች አባባል ሀሳብ ለዘንድሮም ይሠራል፡፡ አሀ…በጊዜ ገብቶ ጋቢ ለብሶ ከሚቀመጥ አባት ይልቅ በጓደኞች ሸክም ተይዞ፣ በሰፈር ልጆች ተሸኝቶ በውድቅት የሚገባ አባት በዝቷላ!
ስሙኝማ…‘ጅብ’ የሚለውን ከጠቀስን አይቀር የሆነ ነገር ትዝ አለኝማ… በዛ ሰሞን የሆነ ኮንዶሚኒየም ላይ ወጥቶ ተገኘ የተባለው ጅብ…አለ አይደል… ከሆነ፣ ልጁን ከሚያስፈራራ አባት ጋር ተማክሮ ነበር እንዴ! ልክ ነዋ…ዘንድሮ እንደሁ የወላጅና የልጅ ግንኙነት አስቸጋሪ እየሆነ ነው፡፡ አንዳንዴ እኮ አንዳንድ ወላጆችን…“ለመሆኑ ልጆችሽ እንዴት አድርገው ነው የሚያሳድጉሽ?” ልንል ምንም አልቀረን፡፡ ማን ማንን እንደሚያሳድግ ግራ እየገባን ነዋ!
ደግሞም ሌላ አለላችሁ…
አንጀቴን አንጀቴ ሲበላው አደረ
አባት የሌለው ልጅ እያንጎራጎረ
እንዲህ ያለ ወራት የተደናገረ
አባቱ በልቶበት ልጁ ጦም አደረ፡፡
አባቶች እየሰለቀጡ ልጆች ጦም የሚያድሩበትን ጊዜ አስወግዶ… ‘የተሻለ’ ጊዜ ያምጣልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

 

 

Published in ባህል

እውቅና ሊያሰጥ የሚችል በጥናት የተደገፈ ማስረጃ ለመንግስት አቅርበናል ብለዋል
መንግስት የህዝቦችን ጥያቄ በህግ አግባብ ምላሽ እንዲሰጥ “ሰመጉ” አሳስቧል

ባለፈው ሳምንት ከጋሞጐፋ ዞን ቁጫ ወረዳ፣ በአንድ መለስተኛ ሎንቺና ተሳፍረው አዲስ አበባ የገቡ 50 የአገር ሽማግሌዎች፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝን ለማነጋገር ከቤተመንግስት ጀርባ ተሰብስበው ነበር፡፡ ሽማግሌዎቹ የቁጫ ወረዳ ህዝብ የራሱ ማንነት፣ ቋንቋ፣ ባህልና አለባበስ ያለው መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ጥያቄያቸው ከአስር አመት በላይ ሲንከባለል ቢቆይም ምላሽ ባለማግኘቱ በጥር ወር 2005 ስለ ወረዳው ህዝብ ማንነት፣እንደ አንድ ብሄር እውቅና ሊያገኝ ስለሚችልባቸው መስፈርቶች፣ ስለ ባህሉ፣ በህዝቡ ላይ ስለተደረጉ ጥናቶችና ውጤቶቻቸው የሚገልፅ ባለ 20 ገፅ ማስረጃ ለፌዴሬሽን ም/ቤት፣ ለጠቅላይ ሚኒስትር ፅ/ቤትና ለኢፌዲሪ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ማስገባታቸውን የአገር ሽማግሌዎቹ ገልፀዋል፡፡ ጉዳዩ ወደ ፌደራል የመጣበትን ምክንያት ሲያስረዱም “የህዝቡ የማንነት ጥያቄ ላለፉት በርካታ አመታት በክልሉና በዞኑ ወደ ጎን በመገፍተሩ ነው” ብለዋል ሽማግሌዎቹ፡፡ ችግሩ እያፈጠጠ የመጣው ደግሞ የቁጫ ተወላጅ ህፃናት በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው በቁጫኛ (ቁጫቶ) መማር ሲገባቸው በጋሞኛ እንዲማሩ በመደረጉና ህዝቡ በግድ “ጋሞ ነህ” እየተባለ እንዲያምን በመገደዱ እንደሆነ እነዚህ የአገር ሽማግሌዎች ተናግረዋል፡፡
ባለፈው ጥር ወር ላይ ጉዳያቸውን ለፌደራል መስሪያ ቤቶች ካስገቡ በኋላ፣ መፍትሄ ይገኛል ብለው ቢጠብቁም የባሰ ነገር መከሰቱን የሚናገሩት ሽማግሌዎቹ፤የህዝቡን የማንነት ጥያቄ ያስተባበሩና የደገፉ የተባሉ 13 ሰዎች ለእስር መዳረጋቸውንና ይሄም የወረዳውን ህዝብ እንዳስቆጣ ገልፀዋል፡፡ የአገር ሽማግሌዎቹ በማስረጃነት አቀረብነው እንደሚሉት የጥናት ውጤት፤ የቁጫ ወረዳ በደቡብ ክልል ጋሞጎፋ ዞን ውስጥ የሚገኝ እና 33 ቀበሌዎችን አካትቶ የያዘ ነው፡፡ ወረዳው በደቡብ ምዕራብ የሚገኝ ሲሆን በስተሰሜን ከወላይታ፣ በስተሰሜን ምዕራብ ከዓውሮ፣ በስተምዕራብ ከጎፋ፣ በስተምስራቅ ከባሮዳ እንዲሁም በስተደቡብ ምስራቅ ከጋሞ የሚዋሰን ነው፡፡ ማዕከላዊ ስታስቲክስ ኤጀንሲ በ2000 ዓ.ም ባወጣው መረጃ፤ የወረዳው ህዝብ ቁጥር ከ200ሺህ በላይ መሆኑን ጠቁሟል፡፡ ወረዳው እንደነጋሞ ካሉት ጎረቤት አካባቢዎች ጋር ተስማምቶ እንደሚኖር የጠቀሱት ሽማግሌዎቹ፤በወረዳው ውስጥ ካሉ 33 ቀበሌዎች ስድስቱ ራሳቸውን ጋሞ ብለው እንደሚያምኑና ከእነሱም ጋር በሰላምና በመግባባት ለረጅም ጊዜ እንደኖሩ፣ አሁንም እየኖሩ መሆናቸውን ያብራራሉ፡፡
ሰኔ 28 ቀን 2005 ዓ.ም 13ቱ ሰዎች ሲታሰሩ ጥያቄው የ13ቱ ብቻ ሳይሆን የ200ሺህ ህዝብ ነው በማለት ከገጠር የመጡ ከአምስት ሺህ በላይ የቁጫ ህዝቦች በወረዳው ዋና ከተማ ሰላም በር ከተማ ተሰብስበው እስር ቤቱን እንዳጨናነቁት የጠቆሙት የወረዳው ሽማግሌዎች፤የአስተዳደሩ ኃላፊዎች ይባስ ብለው ወደ ዞኑ እስር ቤት (አርባ ምንጭ ማረሚያ ቤት) አምጥተው እንዳሰሯቸው ይናገራሉ፡፡ ይሄም ሳያንስ በእለቱ ተቃውሞአቸውን ካሰሙት የወረዳው ህዝቦች መካከል ከ500 በላይ ሰዎች ተይዘው ታስረው እንደነበርና ቀስ በቀስ መለቀቃቸውን የሚገልፁት እኒሁ የአገር ሽማግሌዎች፤ 13ቱ ግን አሁንም ድረስ አለመፈታታቸውን ይናገራሉ፡፡ በሁለተኛው ምዕራፍ ደግሞ የማንነት ጥያቄ አንስታችኋል፣ ደግፋችኋል፣ ህዝብን ለረብሻ አስተባብራችኋል በሚል ተጨማሪ 25 ሰዎች መታሰራቸውን የጠቆሙት ሽማግሌዎቹ፤ የወረዳው ፍ/ቤት የመጀመሪያዎቹ 13 ሰዎችና ተጨማሪዎቹ 25 ሰዎች የዋስ መብታቸው ተከብሮ እንዲፈቱ ለአርባ ምንጭ ማረሚያ ቤት ትዕዛዝ ማስተላለፉን ይናገራሉ - የፍ/ቤቱን ደብዳቤ በማስረጃነት በማቅረብ፡፡ “ይሁን እንጂ የአርባ ምንጭ ማረሚያ ቤት የፍ/ቤቱን ትዕዛዝ ባለማክበር አሁንም ሰዎችን ሊፈታ አልቻለም” ሲሉ ያማርራሉ፡፡ ከዚህም ሌላ ተጨማሪ 50 ሰዎች መታሰራቸውንና በ70 ሰዎች ላይ የመያዣ ትዕዛዝ በመውጣቱ፣ ሰዎቹ ሸሽተው በተለያዩ ቦታዎች መበተናቸውን ሽማግሌዎቹ ይናገራሉ፡፡
የቁጫ ህዝብን ጥያቄ በተመለከተ ሰብዓዊ መብት ጉባኤ (ሰመጉ)፤ “መንግስት የህዝቦችን ጥያቄ በህግ አግባብ ምላሽ ይስጥ” በማለት ያወጣው ልዩ መግለጫ በእጃችን ይገኛል፡፡ መግለጫው ከሐምሌ 28 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ በአርባ ምንጭ ማረሚያ ቤት የሚገኙትን የ13 ሰዎች ስም እና የሥራቸውን ሁኔታ ከገለፀ በኋላ፣ ባልተጣራ ጉዳይ እስር ቤት መግባታቸው ሳያንስ ከስራቸው ለማሰናበት ማስታወቂያ ያወጡባቸው መሆኑን ማረጋገጥ መቻሉን ጠቁሟል፡፡ በጎፋ ዞን ውስጥ የጋሞ፣ጎፋ፣ዘይሴ፣ጊዲቾና አፋይዳ ብሄረሰቦች እውቅና ተሰጥቷቸው እየኖሩ በመሆኑ፣ የቁጫ ህዝብም “ቁጫ ብሄረሰብ” ተብሎ እንደ ስደስተኛ ብሄረሰብ እውቅና ይሰጠን በሚል ያቀረበውን ጥያቄ መንግስት በአግባቡ መርምሮ፣በህግ አግባብ ምላሽ እንዲሰጥ ሰመጉ አሳስቧል፡፡የቁጫ ህዝብ “ቁጫቶ” የተሰኘ ልዩ ቋንቋ እንዳለው፣የአንድ ቋንቋ ቤተሰብ ወይም ተመሳሳይ ቀበሌኛ የሚባለው ከ80 በመቶ በላይ ሲመሳሰል መሆኑን፣.ነገር ግን ቁጫ ቋንቋ ከጋሞ ጋር የሚመሳሰለው ከ77 በመቶ በታች እንደሆነ አቶ ወንድሙ ጋጋ የተባሉ ተመራማሪ ያደረጉትን ጥናት ውጤት በማስረጃነት አቅርበዋል፡፡ አቶ ሀብታሙ ኃ/ጊዮርጊስ የተባሉ የቁጫ ተወላጅና የሶሲዮሎጂና የሶሻል አንትሮሎጂ ምሩቅ በበኩላቸው፣ “ቬንደርና ተባባሪዎቹ የተባሉ የውጪ አገር አጥኚዎች በኦሞቲክ ቋንቋዎች ላይ በሰሩት ጥናት፣ የቁጫን ቋንቋ ራሱን የቻለ አንድ ቋንቋ ነው ብለው አረጋግጠዋል” በማለት ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ አንድ ጃፓናዊ አጥኚም፣ የቁጫ ቋንቋ ጋሞኛንና ቁጫን ድንበር ለድንበር ያሉ ግን የተለያዩ ቋንቋዎች በሚል በጥናታቸው መግለፃቸውን ጨምረው ተናግረዋል፡፡
በኢፌዲሪ ህገ-መንግስት አንቀፅ 39(5) መሰረት፣ የቁጫ ህዝብ እንደ አንድ ብሄር እውቅና ሊያሰጠው የሚያስችለውን መስፈርቶች አሟልቷል የሚሉት ሽማግሌዎቹ፤ ከመስፈርቶቹም መካከል ህዝቡ ከ50 ሺህ በላይ መሆኑ ፣የሥነልቦና አንድነት ያላቸውና በአብዛኛው በተያያዘ መልክአምድር የሚኖሩ መሆናቸው፣ ሰፋ ያለ የጋራ ጠባይ የሚያንፀባርቅ ባህል ወይም ተመሳሳይ ልምዶች ያሏቸው መሆናቸው፣የሚግባቡበት የጋራ ቋንቋ (ቁጫኛ) ያላቸው መሆኑ፣ የጋራ ወይም የተዛመደ ህልውና አለን ብለው የሚያምኑ መሆኑ ሲሆን ህዝቡም በህገመንግስቱ አንቀፅ 39(2) እና (3) መሰረት ጥያቄያችን ምላሽ ሊያገኝ ይገባል፣ይህን የሚሰማን በማጣታችን ወደ ፌደራል መ/ቤቶች ብንመጣም ሊያናግረን የቻለ የለም፣ የፌዴሬሽን ም/ቤት አንድ ሰው አነጋግረውን ነበር፣ ፌደራል በክልሎች ስራ አይገባም፣ ግን ደብዳቤ እንፅፋለን ብለውናል፣ ምንም እልባት ሳናገኝ ወደመጣንበት ተመልሰናል ሲሉ አማርረዋል፡፡
ቁጫ ከ16ኛው ክ/ዘመን አጋማሽ ጀምሮ በ14 ነገስታት ትመራ የነበረች ፣ራሷን የቻለች ባለ ለም መሬት መሆኗን የገለፁት የአገር ሽማግሌዎች፤የታሰሩት ሰዎች ይፈቱልን፣ጥያቄያችን ይመለስ፤ በየቀበሌያችን ገብተው ነፃነት እንዳይሰማን ያደረጉ ታጣቂዎች ይውጡልን፣እንደ አንድ ብሄር ለመታወቅ መስፈርቶችን እናሟላለን፤ ይህን ጠቅላይ ሚኒስትር ኃ/ማርያም ደሳለኝ፣ የፌዴሬሽን ም/ቤት አፈጉባኤ እንዲሁም የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ይስማልን በማለት በርካታ ጥያቄዎችን አቅርበዋል፡፡ “ከዚህ በፊት 50 የአገር ሽማግሌዎች ወደ መዲናዋ መጥተን ጠ/ሚኒስትሩን ለማነጋገር ሞክረን አልተሳካም፣ ሁለተኛውም የአገር ሽማግሌዎች ቡድን ምንም ምላሽ ሳያገኝ በእንግልት ተመልሷል” ያሉት የአገር ሽማግሌ፤ አራት እና ሰባት እየሆኑ ወደ ፌዴራሉ መ/ቤቶች ከሰባት ጊዜ በላይ መጥተው ምላሽ አለማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህ ሁሉ ችግር እየተፈጠረ ያለው የወረዳው አስተዳዳሪዎች በአብዛኛው የጋሞ ተወላጆች በመሆናቸውና ቁጫ እውቅና ካገኘ የስልጣን ወንበራቸው እንዳይነጠቅ በሚፈሩ ባለስልጣናት ነው ብለዋል፡፡“ከዚህ በፊት የወረዳውን ህዝብ ስብሰባ በመጥራትና በማነጋገር በወረዳው ላሉ የጋሞ ተወላጆች እድል በመስጠት ድራማ ሰርተውብናል” ያሉት ሽማግሌዎች፤ጥያቄው የህዝብ ሳይሆን የግለሰቦች ፍላጎት እንደሆነ በማስመሰል መንግስትን ለማሳሳት በደቡብ ቴሌቪዥን የተላለፈውን ፕሮግራም አጥብቀው እንደሚቃወሙ ተናግረዋል፡፡ሽማግሌዎቹ ይህን ይበሉ እንጂ የጋሞ ዴሞክራሲያዊ ህብረት ጉዳዩን በተመለከተ ባወጣው መግለጫ፤ “የጋሞን ህዝብ አንድነት ለመበታተን የተፈፀመ ሴራ ነው” ብሏል፡፡

 

(ነገር ንአጓዲኣ ትልክም፣ ታኼላ ንኣታዊኣ ተስጥም)

ከእለታት አንድ የክረምት ቀን፣ አንዳች አውሎ ንፋስ በመጣ ሰዓት፤ ፈረስ፣ በሬ እና ውሻ አንዱን የሰው ልጅ እንዲያስጠልላቸውና እንዲያሳድራቸው ለመኑት፡፡ ሰውዬው መልካም ፈቃዱ ሆነ፡፡ የክረምቱ ብርድ በርዷቸዋልና ይሞቃቸው ዘንድ እሳት አነደደላቸው፡፡ የሚተኙበት ምቹ ስፍራም ሰጣቸው፡፡ ይበሉት እንዳይቸገሩም ለፈረሱ ገብስ ሰጠው፡፡ ለበሬው ጭድ ሰጠው፡፡ ለውሻውም ከራሱ ራት ከተረፈው ፍርፋሪ አቀረበለት፡፡
በነጋታው ነፋሱ ካቆመ በኋላ ሲለያዩ ምሥጋናቸውን ለሰውዬው ለማቅረብ አሰቡ፡፡
“እንዴት አድርገን እናመስግነው?” አለ ፈረስ፡፡
“የሰውን ልጅ እድሜ እናስላና፤ በየፊናችን ተካፍለን፣ ያለንን ጥሩ ጠባይ ብንሰጥስ?” አለ ውሻ፡፡
“እንዴት ማለትህ ነው?” ሲል ጠየቀ በሬ፡፡
ውሻም፤
“እያንዳንዳችን ልዩ ችሎታ አለን አይደል? ያንን የው ልጅ እድሜ፣ ከእድሜው ጋር በሚሄደው ፀባዩ አንፃር እናጤነዋለን” አለ፡፡
ፈረስ፤
“አሁንም ልትል የፈለግኸው በደንብ አልገባኝም”
ውሻ፤
“ልዘረዝርልህ እኮ ነው፡፡ ለምሳሌ በመጀመሪያ የህይወቱ ክፍል፣ የሰው ልጅ ወጣት ነው፡፡ ለዚህ የሚሆን ጠባይ ማን ይስጠው?” ሲል ጠየቀ፡፡
ፈረስ፤
“እኔ እሰጠዋለሁ” አለና ሰጠ፡፡ በዚህ ረገድ ወጣቶች ሁሉ ትእግስት-የለሽና ጉልበተኛ እንዲሆኑ ሆኑ፡፡
ውሻ ቀጠለና፣
“ቀጥሎ፣ ሁለተኛው የህይወቱ ክፍል የመካከኛ እድሜ ጐልማሳነቱ ነው - ለዚህስ የሚሆን ፀባይ ማን ይስጠው?” አለ፡፡
በሬ፤
“እኔ እሰጠዋለሁ፡፡ የእኔን ጠባይ ይውሰድ” አለ፡፡ እውነትም የሰው ልጅ በመካከለኛ እድሜው በሚሰራው፣ ሥራ ዘላቂ ምን ጊዜም ደከመኝ የማይል፣ ምንጊዜም ታታሪ የሆነ ባህሪ ኖረው፡፡
በመጨረሻም ውሻ፤
“የሽምግልና ጊዜ ጠባይን እኔ እለግሰዋለሁ” አለ፡፡ በዚህም መሰረት የሰው ልጅ በእርጅናው ጊዜ ነጭናጫና በትንሹ የሚያኮርፍ፣ “ውሻ በበላበት ይጮሃል” እንደሚባለው ምግብ ላበላውና ምቾት ለሀጠው የሚያደላና፤ ፀጉረ - ልውጥ ሰው ላይ ግን የሚጮህና የሚናከስ ሆነ፡፡
***
ትእግስት-የለሽና ጉልበተኛ ወጣቶች ለአደጋ ይጋለጣሉ፡፡ ዘላቂና ታታሪ ዜጐች ለሀገር ህልውና ዋና ቁምነገር ናቸው፡፡ የሽማግሌዎች መርጋትና መሰብሰብ፤ ለሀገር የረጋ ህይወት መሰረት ነው፡፡ በአንፃሩ ሽማግሌው ነገር ፈላጊ፣ ጉልቤ ልሁን ባይ፣ የማያረጋጋ ከሆነ የአገር አደጋ ነው፡፡ የፈረሱም፣ የበሬውም፣ የውሻውም ባህሪ በሰው ልጆች ህይወት ውስጥ ወሳኝነት ያላቸው ጉዳዮች እንደመሆናቸው፤ ህብረተሰባችንን ለመመርመር ያግዙናለ፡፡ በየሥራ ምድቡና በየሀብት መደቡ፣ እንዲሁም በአገር አመራር ደረጃ ባሉ ዜጐች ላይም ይንፀባረቃሉና፡፡
የሀገር መሪዎች ወደ አመራሩ ቡድን ፊታቸውን ሲያዞሩ፤ ለህዝቡ ጀርባቸውን መስጠታቸው አይቀሬ ነው ይላሉ የፖለቲካ ፀሐፍት፡፡ ”ከጭምብሉ በስተጀርባ” በተባው መፅሐፍ ደራሲው ባድዊን፤
“ኦርኬስትራውን ለመምራት የሚፈልገው ኅብረ-ዜማ - አቀናጅ (Conductor) ጀርባውን ለተመልካቹ ህዝብ ይሰጣል” ይለናል፡፡
ኦርኬስትራው መስመር ከያዘ በኋላ ግን ወደ ህዝቡ መዞር ያስፈልጋል፡፡ ኦርኬስትራውም የሚያነጣጥረው ተመልካቹ ላይ ነው፡፡ የኅብረ-ዜማውን ቃና ማጣጣም ያለበት ህዝቡ ነው፡፡ ኦርኬስትራውም ሆነ መሪው ኅብረ-ዜማው ለኅሩያን ኅዳጣን (ለጥቂቶች ምርጦች እንዲሉ) ብቻ እንዲሰማ ከሆነ የታቀደው፤ አዲዮስ ዲሞክራሲ!
በሀገራችን እንደተመላላሽ በሽተኛና አልጋ ያዥ በሽተኛ ተብለው ሊከፈሉ የሚችሉ አያሌ ችግሮች አሉ፡፡ አንድኞቹ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሳይገባ በፊት ሲነገሩ፣ ሲመከሩ የሚሰሙ ዜጐች “እሺ፤” ጐርፍ ከመጣም ሲደርስ እናቋርጠዋለን” የሚሉ የሚፈጥሩት ነው፡፡ ሁለተኞቹ ጐርፍ እሚባል ከነጭራሹም ሊመጣ አይችልም፤ የሚሉቱ የሚፈጥሩን ችግር ነው፡፡ ሦስተኞቹ ሀሳቡን ወይም መረጃውን ያመጡትን ክፍሎች “በሬ ወለደ ባዮች” ብለው የሚፈርጁ በመሆናቸው የሚፈጠር፡፡ አራተኞቹ ግን በጣም ጥቂቶቹ ምክር ተቀብለው፤ ድምፅ የላቸውም እንጂ፣ እንጠንቀቅ እያሉ ጥሩ ደወል ቢያሰሙም የመደማመጥ ችግር ነው፡፡ ደጋግመን በከበደ ሚካኤል ልሳን እንደተናገርነው፡- ዛሬም “…አሁን የት ይገኛል ቢፈልጉ ዞሮ
መስማት ከማይፈልግ የባሰ ደንቆሮ”
እንላለን፡፡
እንሰማማ፡፡ ችግሮች ይግቡን፡፡ ቀድመን ሁኔታዎችን እንይ! የቅድመ-አደጋ ጥሪ ማዳመጥን ትተን፤ ጐርፉ ሲመጣ አንጩህ፡፡ ጉዞ እሚሰምረው ነገር ማጣጣም ሲኖር ነው፡፡ ጉዞ ይሳካል እሚባለው ቅድመ-እንቅፋትን ማየት ሲቻል ነው፡፡
እንቀሰቅሳለን ያልነው መንገድ ውሎ ሲያድር ምን እሳት ይዞ እንደሚመጣ እናስተውል፡፡ “እዚያም ቤት እሳት አለ!” ጨዋታ ንግገር አይደለም፡፡ ቀድሞ ማስላት ጉዳት የለውም፡፡ የቀደሙ ስህተቶችንም አውቆ ማረም ነውር አይደለም፡፡ እሳቱ ሲለኮስ ማገዶ ሲጫር ያልነቃ ልቦና፤ ብዙ ጊዜ አደጋ ያስተናግዳል፤ ይባላል፡፡
የተዳፈነ እሳትን ለማንቃት መሞከር አላግባብ ድካም ነው፡፡ ያ እሳት ከተንቀለቀለ ደግሞ ራስንም ጭምር ያነዳል፡፡ ይሄ ማለት ደግሞ፤ እንደትግሪኛው ተረት፤ “ነገር ለጫሪዋ ትተርፋለች፣ ረግረግ የረገጣትን ታሰጥማለች” ማለት ነው፡፡

Published in ርዕሰ አንቀፅ

ማሳወቅ ባለብን ሰዓት አሳውቀናል፤ ለሚፈጠረው ችግር መንግስት ሀላፊነቱን ይወስዳል- ኢ/ር ይልቃል ጌትነት
ሰማያዊ ፓርቲ ሳያስፈቅድ በሚያካሂደው ሰልፍ ለሚፈጠር ችግር ሀላፊነት ይወስዳል- አቶ ሽመልስ ከማል
የሰማያዊ ፓርቲ የነገው ሰልፍ ህገወጥ ነው - ም/ኮሚሽነር ግርማ ካሳ

በነገው እለት ሰማያዊ ፓርቲና የአዲስ አበባ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ በመስቀል አደባባይ ሰላማዊ ሰልፍ የጠሩ ሲሆን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ማሳወቂያ ፅ/ቤት፤ የሰማያዊ ፓርቲ ሰልፍ ህገወጥ ነው ብሏል
ሰላማዊ ሰልፍ ለማካሄድ የሚመለከተውን አካል አሳውቄአለሁ ያለው ሰማያዊ ፓርቲ በበኩሉ፤ ከሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ በፊት ማሳወቁን ገልፆ፤ በሁለት ሰልፎች ምክንያት ለሚፈጠረው ችግር ተጠያቂው መንግሥት ነው ብሏል፡፡
“ሰማያዊ ፓርቲ ሰልፉ አልተፈቀደለትም ያሉት የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል፤ ፓርቲው ይህንን ተላልፎ በሚያካሂደው ሰላማዊ ሰልፍ ለሚፈጠር ማንኛውም ችግር ሀላፊነቱን ይወስዳል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል፡፡
ሰላማዊ ሰልፍ ለማካሄድ የሚፈልግ አካል ሰልፉን ያደራጀውን ሰው፣የሰልፉን አላማ ይዘት፣ የሚወጣውን የሰው መጠን ግምት፣የሚካሄድበትን ጊዜና ቦታ መግለፅ እንዳለበት የጠቀሱት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ይህን ማሳወቅ ብቻ ሳይሆን ማስፈቀድም እንደሚያስፈልግ በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡ “ማሳወቅ ማለት ማስፈቀድ አይደለም” ያሉት አቶ ሽመልስ፤ ካሳወቁም በኋላ ፍቃድ መጠየቅ የግድ ነው ብለዋል፡፡ “በበኩሌ የአዲስ አበባ ሀይማኖት ተቋማት ጉባኤ ፅህፈት ቤት እሁድ የአክራሪነትና የፅንፈኝነት እንቅስቃሴን በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ማስፈቀዱን አውቃለሁ” ያሉት አቶ ሽመልስ፤ በየትኛውም አገር በአንድ ቀንና በአንድ ቦታ ሁለት ሰላማዊ ሰልፎች ማካሄድ ስለማይፈቀድ፣ ፈቃድ ሰጭው አካል ይህን እያወቀ ለሰማያዊ ፓርቲ ፈቃድ ይሰጣል የሚል እምነት የለኝም ብለዋል፡፡ “በመሆኑም ሰልፉን የሚያካሂደው የተፈቀደለት አካል ነው” ብለዋል፡፡ አቶ ሽመልስ አክለውም፤ “በየትኛውም አገር ፍቃድ ሳይገኝ ሰላማዊ ሰልፍ አይወጣም፣ማሳወቅ ብቻ በቂ ነው ብሎ ህግን በመናቅ የትም አይደረስም፣ይህን ተላልፎ ቢገኝ ለሚፈጠረው ችግር ፓርቲው ሀላፊነት እንደሚወስድ ራሱም ያውቀዋል” ብለዋል፡፡ “በአንድ ቀን ሁለት ሰላማዊ ሰልፎች የማይፈቀዱት የተለያዩ ግጭቶች እንዳይፈጠሩ፣ የትራፊክ መጨናነቅ እንዳይፈጠርና የፀጥታ ሀይሎች ወደተለያዩ ስራዎች ሊሰማሩ ስለሚችሉ የፀጥታ ችግር እንዳይከሰት ነው” ሲሉ አቶ ሽመልስ ገልፀዋል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በበኩላቸው፤ ፓርቲያቸው ከሶስት ወር በፊት በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ያነሳቸው የህዝብ ጥያቄዎች ካልተመለሱ፣ ከሶስት ወር በኋላ ሁለተኛውን ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚጠራ በተደጋጋሚ መግለፃቸውን አስታውሰው፤ ይህም ጊዜ ነገ መሆኑንና አስፈላጊውን መስፈርት ማሟላታቸውን ተናግረዋል፡፡ “እኛ የማሳወቂያ ደብዳቤውን ያስገባነው ከሀይማኖት ተቋማት ጉባኤ ፅ/ቤት በፊት ነው” ያሉት ኢ/ር ይልቃል፤ መንግስት በእኛ ላይ የተደረበውን ሰላማዊ ሰልፍ መሰረዝ እንዳለበት በመግለጫ ማሳወቃቸውንና ሰልፉን ከማካሄድ የሚገታቸው እንደሌለ ተናግረዋል፡፡ “ሁለት ሰላማዊ ሰልፎች ሲካሄዱ ለሚፈጠረው ችግር መንግስት ሀላፊነቱን ይወስዳል” ሲሉም አሳስበዋል፡፡
ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰልፍና ስብሰባ ማሳወቂያ ፅ/ቤት የማሳወቂያ ደብዳቤውን ካስገቡ በኋላ ፅ/ቤቱ የስብሰባውን አላማ፣የትና መቼ እንደሚያካሂዱ፣የሰው ብዛት ምን ያህል እንደሚገመት ፓርቲው እንዲያሳውቀው በደብዳቤ በጠየቀው መሰረት ለጥያቄዎቹ ሁሉ በደብዳቤ ምላሽ መስጠታቸውን ኢ/ር ይልቃል አስታውሰው፤ ነገር ግን ማሳወቂያ ፅ/ቤቱ በ48 ሰዓት ውስጥ ምላሽ ባለመስጠቱ እንደተፈቀደ ቆጥረን ዝግጅታችንን አጠናቀናል ብለዋል፡፡ በመሆኑም ከሰማያዊ ፓርቲ በኋላ መጥቶ ሰልፍ የሚያካሂደውን አካል በማስቆም፣ መንግስት ሀላፊነቱን መወጣት አለበት ብለዋል - የፓርቲው ሊቀመንበር፡፡የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ማሳወቂያ ፅ/ቤት ሀላፊ አቶ ማርቆስ ብዙነህ፤ “እኔ የማውቀው አንድ ሰላማዊ ሰልፍ ነው፤ የሰማያዊ ፓርቲ ህገወጥ ነው” በማለት መልሰዋል፡፡ ሌላ ሰላማዊ ሰልፍ በዕለቱ ስለመካሄዱ ለፓርቲው አሳውቀው እንደሆነ የተጠየቁት አቶ ማርቆስ፤ “ደብዳቤ ፅፈን ስንሰጣቸው የፓርቲው ሰዎች አንቀበልም በሚል ወርውረውት ሄደዋል” ብለዋል፡፡ ጉዳዩን አስመልክተን የጠየቅናቸው የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል፤ “ፅ/ቤቱ በቃልም በደብዳቤም ያሳወቀን ነገር የለም፤ እኛም በነገው ዕለት ሰልፉን እናካሂዳለን” በማለት የፅ/ቤቱን ምላሽ አጣጥለውታል፡፡ ትናንትና ረፋድ ላይ አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ጠርቶ እንዳነጋገራቸው የገለፁት ኢ/ር ይልቃል፤ “ሰላማዊ ሰልፍ እንደምታካሂዱ የደረሰን መረጃ የለም” መባላቸውን ጠቁመው፤ ማሟላት ያለባቸውን መስፈርት እንዳሟሉ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ም/ኮሚሽነር ግርማ ካሳ አሳውቀው መውጣታቸውን ተናግረዋል፡፡ በስልክ ያነጋገርናቸው ም/ኮሚሽነር ግርማ ካሳ፤ ሰማያዊ ፓርቲ ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚያካሂድ ከሚመለከተው አካል ደብዳቤ እንዳልደረሳቸው ገልፀው፣ ሰማያዊ ፓርቲም ሰልፉ የተፈቀደበትን ማስረጃ ማቅረብ እንዳልቻለ ተናግረዋል፡፡ “በመሆኑም የነገው የሰማያዊ ፓርቲ ሰላማዊ ሰልፍ ህገ ወጥ ነው” ሲሉ አረጋግጠዋል፡፡

 

Published in ዜና

የኢትዮያ አየር መንገድ ባለቀው በጀት ዓመት ከምንጊዜውም በላይ የላቀ ትርፍ ማስመዝገቡን አስታወቀ፡፡
የአየር መንገዱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገ/ማርያም እንደገለፁት፤ አየር መንገዱ በበጀት ዓመቱ ከምንጊዜው የላቀ የ2.03 ቢሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ አግኝቷል፡፡ ትርፉ ከአምናው 734 ሚሊዮን ብር ጋር ሲነፃፀር 178 በመቶ ዕድገት መመዝገቡን ዋና ሥራ አስፈፃሚው ገልፀዋል፡፡
በበጀት ዓመቱ ከሰውና ከዕቃ ማጓጓዝ የተገኘው 38.5 ቢሊዮን ብር ገቢ ከአምናው 33.8 ቢሊዮን ብር ጋር ሲነፃፀር የ14 በመቶ ብልጫ እንዳለው፣ እንዲሁም ሰውና ዕቃ ከማጓጓዝ የተገኘው 2.7 ቢለዮን ብር ለፕሬቲንግ ፕሮፊት ከአምናው 1.0 ቢሊዮን ጋር ሲነፃር የ165 በመቶ ብልጫ ማሳየቱን ተናግረዋል፡፡
የአየር መንገዱ የተጣራ ትርፍ ከዓለም አቀፍና ከአፍሪካ የአውሮፕላን ኢንዱስትሪ አማካይ የተጣራ ትርፍ ጋር ሲነፃፀር ከፍተኛ መሆኑን የገለፁት አቶ ተወልደ፤ የአፍሪካ የተጣራ ትርፍ 0.9 በመቶ፣ የዓለም አቀፍ ደግሞ 1.8 በመቶ ሲሆን የኢትዮጵያ አየር መንገድ 5.3 በመቶ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ አየር መንገዱ ለዚህ ውጤት የበቃው በሠራተኛውና በማኔጅመንቱ ብልህ አመራርና ቆራጥነት፣ ትክክለኛ የረዥም ጊዜ ስትራቴጂ፣ በአፍሪካና በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ዕድገት በመዝገቡና ደንበኞቹ እምነት ሰጥተው ስለሚመርጡት…እንደሆነ ሥራ አስፈጻሚው ተናግረዋል፡፡ ለአየር መንገዱ ዕድገት ሌላው ምክንያት የዘጠኝ አዳዲስ መዳረሻዎች መከፈትና የነባሮቹም የምልልስ ጊዜ መጨመር እንደሆነ ጠቅሰዋል፡፡ አየር መንገዱ፣ የማርኬቲንግና የሰው ኃይል አቅም ግንባታ ማሠልጠኛ ሕንፃ 95 በመቶ መጠናቀቁን፤ አዲስ ተርሚናልና ዕቃ ማቆያ ለመገንባት ፋይናንስ በመፈለግና የዲዛይን ሥራ መጀመሩን የጠቆሙት ሥራ አስፈፃሚው፤ ለባለ 4 ኮከብ ሆቴል ግንባታ የብድር ስምምነት እየተካሄደ መሆኑንም ገልፀዋል፡፡ ለአየር መንገድ ሠራተኞች የ1192 ቤቶች ግንባታ 30 በመቶ በሚቀጥለው ዓመት እንደሚጠናቀቅ የጠቀሱ ሲሆን ባለፈው ወር ለሠራተኞቹ እንደየስኬሉ ከ6 እስከ 8 ደረጃ የደሞዝ ጭማሪና የአንድ ወር ደሞዝ ቦነስ መስጠቱ ታውቋል፡፡
ባለፈው ጥርም ለእያንዳንዱ ሠራተኛ እንደየስኬሉ ከ15 እስከ 25 በመቶ የደሞዝ ጭማሪ መደረጉ ታውቋል፡፡

Published in ዜና

አቶ መላኩ ፋንታ እና አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስ በ3 መዝገቦች ተከሰዋል
ሶስት ተጠርጣሪዎች በነፃ ተለቀዋል

የፌደራሉ የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን አቃቤ ህግ፤ ከ40 በላይ በሚሆኑ የገቢዎችና ጉምሩክ መስሪያ ቤት ባለስልጣናት እና የቅርንጫፉ ጽ/ቤት ሠራተኞች እንዲሁም ከባለስልጣናቱና ሠራተኞች ጋር ተመሳጥረው ከባድ የሙስና ወንጀል ፈጽመዋል በተባሉት ባለሀብቶች ላይ 8 የክስ መዝገቦች አደራጅቶ ከፈተ፡፡ በምርመራ ቀጠሮ ላይ የቆዩ 3 ተጠርጣሪዎች በነፃ ሲለቀቁ፣ ቀደም ሲል በዋለው ችሎት ምርመራቸው አልተጠናቀቀም ተብለው እንደገና ወደ ምርመራ ቀጠሮ የተመለሱት ተጠርጣሪዎች ባሉበት ሆነው እስከ ጳጉሜ 1 ቀን 2005 የምርመራ ስራው እንዲቀጥል ተብሏል፡፡
የኮሚሽኑ አቃቤ ህግ በተከሳሾቹ ላይ የከፈታቸው 8 መዝገቦች በሚኒስትር ማዕረግ የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር የነበሩት አቶ መላኩ ፋንታ እና አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስ በሶስት መዝገቦች ክስ ቀርቦባቸዋል፡፡
የተከሳሽ ጠበቆች በየደንበኞቻቸው ላይ የቀረበው የክስ ጭብጥ እንዲሰጣቸው የጠየቁ ቢሆንም ፍ/ቤቱ እስከቀጠሮ ባለው ጊዜ ውስጥ እንዲደርሳችሁ ይደረጋል የሚል ምላሽ ሰጥቷል፡፡ ተከሳሾችም በቀጣይ ቀጠሮ ሲቀርቡ የክሱ ጭብጥ እንደሚነበብላቸው ተገልጿል፡፡
የኮሚሽኑ መርማሪ ቡድን፤ የባለስልጣኑ ሠራተኞች በነበሩት በአቶ ንጉሴ ክብረት፣ አቶ ጌታቸው አሰፋ እና አቶ ምሣሌ ወ/ስላሴ ላይ ሲያካሂድ የነበረውን ምርመራ በማጠናቀቁና ክስ እንደማይመሰረትባቸው በማረጋገጡ በነፃ እንዲለቀቁለት ጠይቆ፣ ፍ/ቤቱ እንዲለቀቁ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ በሌላ በኩል በእነ አቶ ገ/ዋህድ መዝገብ ተካተው ምርመራ ሲካሄድባቸው የነበሩት አቶ ሙሌ ጋሻው በመሃንዲስነት ሲሰሩ በነበሩበት የኦሮሚያ ክልል ፍ/ቤት ጉዳያቸው እንዲታይ አቃቤ ህግ አመልክቷል፡፡ ተጠርጣሪውም ፈቃደኛነታቸውን በመግለጻቸው ፍ/ቤቱ የአቃቤ ህግን ጥያቄ ተቀብሎ ጉዳያቸው በክልሉ ፍ/ቤት እንዲታይ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል የኦዲት ምርመራው ባለመጠናቀቁ አቃቤ ህግ፣ በአቶ ተክለአብ ዘረአብሩክ፤ አቶ ምህረተአብ አብርሃ፣ አቶ በእግዚአብሔር አለበል እና አቶ ፍፁም ገ/ማርያም ላይ የ14 ቀን ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ የጠየቀ ቢሆንም ፍ/ቤቱ ከተጠየቀው ጊዜ ቀጠሮ 8 ቀን ብቻ በመፍቀድ ተጠርጣሪዎች ባሉበት ማረፊያ ቤት ቆይተው ለጳጉሜ 1 ቀን 2005 እንዲቀርቡ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
የክስ መዝገብ የተከፈተባቸውን ተጠርጣሪዎች በ15ኛ ወንጀል ችሎት በኩል ክሳቸው እንዲታይ ለጥቅምት 11 እና 12 ቀን 2005 ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

Published in ዜና
  • “አዘጋጁን አስፈቅደን ያደረግነው ስለሆነ ችግር የለውም” 
  • - አቶ ሳሙኤል ተስፋዬ (የቴአትር ክፍል ኃላፊ)

በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቴአትር ቤት የሚሰሩ ተዋንያን ቅዳሜ በቋሚነት የሚታይ ቴአትር ተቋርጦ ሌላ ፕሮግራም መካሄዱ ከቴአትር ስነ-ምግባር ጋር የሚቃረን ነው ሲሉ ቅሬታቸውን አሰሙ፡፡ በዛሬው ዕለት ትያትር ተቋርጦ በብሔራዊ ቴአትር የሚካሄደው ፕሮግራም የቴአትር ቤቱን ችግሮች ለመፍታት ያለመ ነው ተብሏል፡፡ የፕሮግራሙ አላማ የተቀደሰ ቢሆንም ቴአትር ማቋረጥ የሞያውንም ሆነ የሞያተኛውን ክብር የሚነካ ነው ብለዋል - ተዋንያኑ፡
የቴአትር ቤቱ የቴአትር ክፍል ኃላፊ አቶ ሳሙኤል ተስፋዬ በበኩላቸው፤ ዋናው ጉዳይ አዘጋጁን ማስፈቀድና አዘጋጁ መፍቀዱ መሆኑን ገልፀው፤ የቴአትሩን አዘጋጅ አርቲስት ጌትነት እንየውን የቴአትር ቤቱ አመራሮች ስላስፈቀዱት ችግር እንደሌለው ገልፀዋል፡፡
ተዋንያኑ በበኩላቸው፤ የሙያው መርህ “The show must go on” የሚል በመሆኑ ዝግጅቱን በሌላ ቀን ማካሄድ እየተቻለ ቅዳሜ ማድረግ ሙያውን የሚያንኳስስ ነው ብለዋል፡፡ አንድ ተዋናይ የመድረክ ስራ እያለው እናቱ ብትሞት እንኳን መቅበር አይችልም ያሉት ተዋንያኑ፤ ምንም ቢሆን ቴአትር መቋረጥ እንደሌለበት ተናግረዋል፡፡
“እኛ የቴትር ቤቱን አካሄድና አሰራር ለማሻሻል የተያዘውን ፕሮግራም አልተቃወምንም፤ ነገር ግን የውይይትና የግብዣ ፕሮግራሙ በሌላ ቀን መሆን ሲችል ቴአትሩን አቋርጦ ማካሄዱ አግባብ አይደለም” ሲሉ ተቃውመዋል፡፡
“የሰውን “ህይወት በአደራ ይዞ የሚሰራው የህክምና ዶ/ር እንኳን ቤተሰብ ቢሞትበት ሌላ ዶ/ር ቀይሮ ቤተሰቡን መቅበር ይችላል” ያሉት ባለሙያዎቹ፤ በቴአትር ሙያ ግን ማንንም መተካት፣ ስራ አቁሞ ዘመድ መቅበርም አይቻልም ብለዋል፡፡
የቴአትር ቤቱ የቴአትር ክፍል ኃላፊ አቶ ሳሙኤል በበኩላቸው፤ ቴአትሩ እንዳይቋረጥ ዝግጅቱ ሊካሄድ የነበረው ሀሙስ ቀን እንደነበር አስታውሰው፤ ከአቅም በላይ በሆነ ችግር የሀሙሱ ባለመሳካቱ ለዛሬ መዛወሩን ገልፀዋል፡፡
የፕሮግራሙ ዋና አላማ ቴአትር ቤቱ መስራት ባለበት መጠን ባለመስራቱና የታለመለትን ግብ ባለመምታቱ፣ ለዚህ ችግር እልባት ለመስጠት የተዘጋጀና ለሙያውም ሆነ ለባለሙያው ክብር ትኩረት የሰጠ ፕሮግራም እንደሆነ ያብራሩት አቶ ሳሙኤል፤ ጉዳዩ በበጐ መልኩ ሊታይ ይገባል ብለዋል፡፡
ከዚህ በፊት ቴአትር ቤቱን ይመሩ በነበሩት አቶ አዳፍሬ ብዙነህ ጊዜ ለአርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ “አባይ ወይስ ቬጋስ” ፊልም ምርቃት ቴአትር ቤቱን በመፍቀዳቸው ከፍተኛ ወቀሳና ትችት እንደደረሰባቸው ያስታወሱት ተዋንያኑ፤ ይህን ድርጊት ከተቃወሙት ውስጥ አንዱ የአሁኑ የትያትር ቤቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ተስፋዬ ሽመልስ እንደነበሩ ተናግረዋል፡፡በጉዳዩ ዙሪያ ያነጋገርናቸው የቴአትር ቤቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ተስፋዬ ሽመልስ፤ “ይሄ በፊትም ያለ ነው፤ ኮሚቴውን አነጋግሩ” በማለት አስተያየት ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡ የቴትሩን አዘጋጅ አርቲስት ጌትነት እንየውን ለማነጋገር ያደረግነው ጥረት ሳይሳካልን ቀርቷል፡፡

Published in ዜና

አቢሲኒያ ባንክ ዘንድሮ 351.2 ሚሊዮን ብር አጠቃላይ ትርፍ ማግኘቱንና ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ12.2 በመቶ ብልጫ እንዳለው ገለፀ፡፡ ባንኩ በላከው መግለጫ ላይ እንዳስታወቀው፤ የባንኩ አጠቃላይ ገቢ 895 ሚሊዮን ብር መድረሱንና ካለፈው ዓመት በ126 ሚሊዮን ብር ብልጫ ያለው መሆኑን ጠቁሟል፡፡ ለተለያዩ የንግድና አገልግሎት ዘርፎች በአጠቃላይ 4.7 ቢሊዮን ብር ብድር የሰጠ መሆኑን የገለፀው ባንኩ፤ አጠቃላይ ተቀማጭ ሂሣቡ 8.5 ቢሊዮን ብር መድረሱን አስታውቋል፡፡ አቢሲኒያ ባንክ 371ሺ 420 የሚሆኑ የገንዘብ አስቀማጭ ደንበኞች እንዳሉት መግለጫው ጠቅሶ፤ በተለያዩ የአገሪቱ ከተሞችና ክልሎች 82 የሚደርሱ ቅርንጫፎችን ከፍቶ ለደንበኞቹ አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡

Published in ዜና
Saturday, 31 August 2013 11:48

አገሬ፣ እኔ እናሻማ!

መሸ
ቤቴ ገባሁ፡፡
ያው ደሞ እንዳመሉ
እንደባህሉ ሁሉ …መብራቱ ጨልሟል፡፡
እና ሻማ ገዛሁ
በሻማው ብርሃን፣ ልፀዳበት አሰብሁ፡፡
እና ሻማ ገዛሁ…ሁሉንም ባይሆንም
አንድ ሁለት አበራሁ
በሻማው ብርሃን …መንፈሴን አፀዳሁ
እንደ አያቴ መስቀል
እንደሼኪው ሙሰባህ
እንደ አበው መቁጠሪያ
እንደአገሬ ማተብ …እንዳገሬ ክታብ
አምኜ ጀመርኩኝ፣ ማስታወሻ መፃፍ
ህይወት ባገኝ ብዬ፣ ከጨለማው ደጃፍ፡፡

ከሐምሌ ጨለማ
ከጨረቃዋ ሥር፣ ጉም ከተናነቃት
ክረምቱ ዘንቦባት
ብርድ እንደዛር - ውላጅ፣ እያንቀጠቀጣት፤
አገሬ ጨልማ፤
በእንግድነት ቤቴ፣ መጥታ ልትጠይቀኝ
“መብራቴን ሸጫለሁ፣ ሻማ ለኩስልኝ”
ብላ ለመነችኝ፡፡
“የሸጥሽበት ገንዘብ፣ የት ደረሰ?” አልኳትኝ፡፡
(ይሄኔ ነጋዴ ኖሮ ቢሆን ኖሮ፤ “አትርፋለች?” ባለኝ፡፡
ይሄኔ አንድ ምሁር፣ ኖሮ ቢሆን ኖሮ
ማን ፈቅዶ ነው ይሄ፣ ምን ‘ማንዴት’ አላቸው?
ጉድ መጣ ዘንድሮ፤
ኖሮ ቢሆን ኖሮ፣ የጋዜጣ አንባቢ፤
“ህዝብ ያቃል ይሄንን?
ደባ ሲሰሩ ነው!” ባለ ነበር ምሩን
ሁሉን አስባበት፣ ሻማዊ ሳቅ ሳቀች
ሁሉን አስቤበት፤ ሻማዊ ሳቅ ሳኩኝ፡፡

ከነልብሴ ተኛሁ፣ ብርድ ልብስም የለኝ፡፡
እሷም ሌጣዋን ነች፤ ጐኔ ገለል አለች፡፡
ልክ ዐይኔን ስከድን፣ ቀና አለች ወደኔ
“ሻማውን አጥፋ እንጂ፤ ለነገ አታስብም?
የቁጠባ ባህል፣ ዛሬም አልገባህም?!”
ስትል ገሰፀችኝ፡፡

ሻማው ሰማ ይሄንን፣ ጣልቃ ገባ እንዲህ ሲል
“መብራት ከሄደበት፣ እስኪመለስ ድረስ
ዓመት ፍቃድ ላይ ነኝ፣ ይሁን ልሥራ ለነብስ
የበራሁ መስዬ፣ ተዉኝ ትንሽ ላልቅስ!
ብቻ ወዳጆቼ፤
እንሰነባበት፣ እንሳሳም በቃ፤
ስለማይታወቅ፣ ነግ ማን እንደሚከስም
ነግ ማ እንደሚነቃ!!”
(የነገን ማን ያውቃል ለሚሉ)
ከግንቦት 2004-2005 ዓ.ም

Published in የግጥም ጥግ
Page 3 of 17