አቶ ሽመልስ ከማል፤ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ
መንግስት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተቃዋሚ ፓርቲዎች እየተካሄዱ ስላሉ ስብሰባዎችና ሰላማዊ ሰልፎች ምን ይላል? በተለይ አንድነት ፓርቲ የፀረሽብር ህጉን ለማሰረዝ የሚያደርገውን እንቅስቃሴ እንዴት ያየዋል? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ ከሆኑት አቶ ሽመልስ ከማል ጋር በእነዚህና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ አጭር ቃለምልልስ አድርጓል፡፡

በተቃዋሚ ፓርቲዎች እየተካሄዱ ስላሉ ሰላማዊ ሰልፎች የመንግስት አቋም ምንድነው?
ህገ መንግስቱ በሚፈቅደው መልኩ ማንም ሰው በፖለቲካ የመደራጀት መብት አለው፡፡ ዝም ብለን ካየነው ህገመንግስታዊ መብትን ተጠቅሞ ሃሳብን መግለጽ ነው፡፡ ይህን መብት የማጣጣምና የመጠቀም ጉዳይ ነው፡፡ ተቃዋሚዎች ባይቃወሙና ባይሰባሰቡ ነው እንጂ የሚደንቀው ይህን ማድረጋቸው ብዙም የሚያስደንቅ አይደለም፡፡ ነገር ግን ከሚያነሷቸው ጉዳዮች ውስጥ የበርካታ ዜጐች ስጋት የሆኑ ጉዳዮችም አሉ፡፡ በተለይ ከአክራሪ ጽንፈኛ ሙስሊም ቡድኖች ጋር አንዳንድ ፓርቲዎች የፈፀሙት ያልተቀደሰ ጋብቻ አሳሳቢ ነው፡፡ በሀገራችን ህገመንግስትም ፖለቲካ እና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው፡፡ የፖለቲካ ስብሰባዎች፣ የፖለቲካ ሰልፎች እንኳን ሃይማኖተኞችን ሊቀላቅሉ፣ የሃይማኖት ተግባራት ከሚፈፀምባቸው ቦታዎች በተወሰነ ርቀት መሆን አለባቸው፡፡ አሁን ግን ሁለቱ መቀያየጥ የሌለባቸውን ነገሮች ሲያካሂዱ እያየናቸው ነው፡፡ ይሄ ለነሱም ሆነ ለማንም የሚበጅ አይደለም፡፡ ተገቢ ያልሆነ ህገመንግስቱን የሚፈታተን አካሄድ ነው የሚል እምነት አለን፡፡ ይህ ተግባር የህግን የበላይነት የሚፈታተን መሆኑን አውቀው እርምጃቸውን ማስተካከልና መታረም አለባቸው ማለት ነው፡፡ ህገመንግስቱ ያሰመረባቸው ቀይ መስመሮች መታለፍ የለባቸውም፡፡ በሌላ በኩል ይሄ ስጋት ጽንፈኛ አክራሪነት የአለም ስጋት የሆነበት ዘመን ላይ ነው ያለነው፡፡ ይህን መነሻ አድርጐ ርካሽ ተወዳጅነት ለማግኘትና ጊዜያዊ ጥቅምን ለማግኘት የሚያስቡ ሃይሎችን ማወደስና ከእነዚህ ጋር መተቃቀፍ ለማንም የሚጠቅም አይደለም፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ በርካታ የሀገራችን ሙስሊሞች የማንም መጠቀሚያ አንሆንም እያሉ በአደባባይ ሲናገሩ እያየናቸው ነው፡፡ በየአደባባዩ የጠሩትና ሚሊዮኖችን እናስከትላለን ብለው የለፈፉለት ሰላማዊ ሰልፍ፣ በመቶዎችና በአርባዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ይዞላቸው ሲመጣ ያዩ ተቃዋሚዎች፣ ሌላ ሃይል እናገኝበታለን ብለው የገቡበት ስሌት አደገኛ ስሌት ነው፡፡ ከሽብርተኝነት ጋር የተፈጠረ ድሪያ ነው የሚሆነው፡፡ እንዲህ አይነቱን ነገር ሊጠነቀቁ ይገባቸዋል፡፡ መጥፎ አካሄድ ነው፡፡ ካለፈው ስህተታቸው ትምህርት መውሰድ አለባቸው፡፡ ህገመንግስቱ ሲጣስ ዳር ቆሞ የሚመለከት መንግስት አይደለም ያለው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ በህግ ተወስኖባቸውና ተፈርዶባቸው አሸባሪ ተብለው በፍ/ቤት የተረጋገጠባቸውን ሰዎች፣ እንደሰማዕታት አድርጐ መደገፍ፣ አሸባሪነትን መደገፍ ነው፡፡ ይሄ ለሽብርተኝነት እውቅና መስጠት ማለት ነው፡፡ ከወንጀል ጋር በሚያደርጉት ድሪያ ባህሪያቸውን እያሳዩ ነው፡፡ ወንጀል ጠቀስ የሆኑ ጉዳዮችን እየነካኩ መሄድ አንደኛው ባህርያቸው መሆኑን የሰሞኑ ድርጊታቸው ማሳያ ነው፡፡ አባሎቻቸው እንኳ ሽብርተኛ ሆነው ከተገኙ ራሳቸውን መነጠል ነው ያለባቸው፡፡
በሠልፎቹ ከሚጠየቁት ጉዳዮች መካከል መንግስት ምላሽ ያሻቸዋል ብሎ የተቀበላቸው የሉም? በተለይ ከሰብአዊ መብት አያያዝ ጋር የሚነሱ ጥያቄዎች ላይ?
ዝም ብሎ ለፕሮፖጋንዳ ፍጆታ የሚያነሷቸው ካልሆነ በቀር፣ በሰብአዊ መብት አያያዝ በኩል መንግስት የዜጐችን የሰብአዊ መብት አያያዝ አተገባበር በጣም በተጠናከረ መልኩ እያሻሻለና አድማሱን እያሰፋ በመሄድ፣በቅርቡ የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት አያያዝ መተግበሪያ (አክሽን ፕላን) ያወጣ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዚያ ላይ የእያንዳንዱን ዜጋ ዲሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብት ጥበቃ ለማስተግበር የሚያስችሉ ዝርዝር መርሃ ግብሮችን ነው ያወጣው፡፡ ተቋማት ያለባቸውን ችግሮች በተጨባጭ አይቷል፡፡ ለዚህም መወሰድ ያለባቸውን መፍትሔዎች በግልጽ አስቀምጧል፡፡ ስለዚህ የዜጐችን ሰብአዊ መብት ለመጠበቅና አያያዙን ለማዳበር ተግቶ የሚሰራ መንግስት መሆኑ ግልጽ ነው፡፡
ዝም ብሎ ከዳር ወጥቶ ማረጋገጫ የሌለውን ነገር መናገር ተገቢ አይደለም፡፡ መንግስትን የሰብአዊ መብት አጠባበቅ ከአደባባይ መፈክርና ከአንደበት ግልጋሎት በተረፈ በጣም የሚያሳስበው ጉዳይ መሆኑን አውቆ፣ ከፖሊሲ አፈፃፀሞቹ ጋር አመጋግቦ ተግባራዊ ለማድረግ በመንቀሳቀስ ላይ ነው፡፡
በተለያዩ ከተሞች እየተካሄዱ ያሉት ሰላማዊ ሰልፎች እና ህዝባዊ ስብሰባዎች በመንግስት ላይ ጫና የመፍጠር አቅም የላቸውም?
እንዴት ነው የሚፈጥሩት! ጐንደር በጠሩት ሰልፍ ላይ 200 የሚሆን ሰው ነው የተገኘው፡፡ በሌሎችም ቦታዎች ተመሳሳይ ነው፡፡ እነሱ “ለምንድነው ስብሰባችን ባዶ የሆነው?”፣ “አዳራሻችን ባዶ የሆነው?” ብለው መጠየቅ አለባቸው፡፡ ጣታቸውን ወደ ውጪ ከመደንቆር ይልቅ የህዝቡን ፍላጐት ማየትና ወደ ውስጣቸው መመልከት አለባቸው፡፡ መንግስት እንኳንስ በጣት የሚቆጠሩ ደጋፊዎች ወጥተው ቀርቶ፣ በማንኛውም ሁኔታ ህጋዊ ስራውን ከመስራት የሚያግደው ሃይል አይኖርም፡፡ በመርህ ደረጃ ሃሳብን ይዞ ለመውጣት ቁጥር ወሳኝ ነው የሚል ድምዳሜ ባይኖረኝም፣ በመርህ ደረጃ የሚታየው እውነታው ነው፡፡
መንግስት ተጨባጭ የሆኑ ጥቆማዎችና አስተያየቶች ሲደርሱት ቁጥራቸውን ወሳኝ አያደርገውም፡፡ ያም ሆነ ይህ ግን እነዚህ ሰልፎች ያረጋገጡት ማህበራዊ መሠረታቸው እጅግ ጠባብ መሆኑንና ህዝባዊ ድጋፍና ይሁንታ የሌላቸው መሆኑን ነው፡፡ ነገር ግን ይህን ለመሸፋፈን መንግስት ጫና በማድረጉ ሰው ሊወጣልን አልቻለም ሲሉ ነው የሚደመጡት፣ ይሄ መሠረት የሌለው ውንጀላ ነው።
አንድነት ፓርቲ የፀረ ሽብር አዋጁን በማሰረዝ የሚሊዮኖችን ድምጽ እያሰባሰበ ነው፡፡ የሚሰባሰበው ድምጽ አዋጁን ሊያሰርዘው ይችላል?
በይሆናል እና በግምት የሚሰጥ መልስ የለም፡፡ የፀረ ሽብር ህጋችን ከተለያዩ የአለም ሀገራት ተጠንቶ የተቀረፀ ነው፡፡ የዜጐቻችንን ደህንነት ከሽብር ጥቃት ለመከላከል የህግ ከለላ ያስፈልግ ነበር፡፡ በዚህ መሠረት ህጉ ተቀርጿል፡፡ በህጉም እስካሁን ሊከሰቱ ይችሉ የነበሩ አያሌ ሙከራዎችን ማክሸፍ ችለናል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ስጋት የሚገባቸው ወገኖች እነማን እንደሆኑ ጥርጥር የለውም፣ ዜጐች ግን ስጋት ላይ አይወድቁም፡፡ ህጋዊ ፓርቲዎችንም ስጋት ላይ አይጥልም፡፡ ተገቢ የሆነውንና ያልሆነውን አጣቅሶ ለመሄድ ያሰበ ካለ ግን ድንጋጌው ስጋት ላይ ሊጥለው ይችላል፡፡ ዜጐች ግን ሙሉ ድጋፍ የሰጡት ህግ ነው፡፡
ህጉን ድምጽ በማሰባሰብ ማሰረዝ አይቻልም ማለት ነው?
የህግ አወጣጥ ስርአት በህገመንግስቱ የተደነገገ ነው፡፡ ህግ የሚወጣው በህግ አውጪ አካላት ነው። እነዚህ አካላት ከማውጣቱ ባሻገር ህጉን መሻርም ማሻሻልም ይችላሉ፡፡ እነዚህ ድርጅቶች የህግ የበላይነት ለማክበርና ለህገመንግስታዊ ስርአት እውቅና ለመስጠት የሚያንገሸግሻቸው ተቋማት እንደሆኑ እናውቃለን፡፡ ህገመንግስታዊ ተቋማትንና ህጋዊ አሠራሮችን ለመቀበል የማይፈልጉ ፓርቲዎች ናቸው ይህን የሚያደርጉት፡፡ የፈለጉትን የመመኘትና የማለም መብት አላቸው፣ ለምን አለማችሁ ተብለው አይጠየቁም፡፡ ለዚህ ሰፊ ነፃነትና የፖለቲካ ምህዳር አለ፡፡ ስለዚህ ማለምና ማሰብ ይችላሉ፡፡

(የሚከተለውን ተረት - መሰል ታሪክ ከዚህ ቀደም ትንሽ ለየት ባለ መልኩ ተርከነዋል፡፡ የሚሰማ ጠፍቶ ታሪክ ሲደገም በማየታችን ደግመን አቅርበነዋል፡፡)
አንድ ፀሐፊ እንዳለው “እኔን ቅር የሚለኝ ታሪክ መደገሙ ሳይሆን፤ በበለጠ አስከፊ መልኩ መደገሙ ነው” ይላል፡፡
ዕውነት ሆነው ከመቆየት ብዛት ተረት የሚሆኑ ታሪኮች አሉ፡፡
ባለፈው ሥርዓት፣ ከዕለታት አንድ ቀን የነበሩ፤ ሁለት የትግል ጓዶች ነበሩ አሉ፡፡ ከጊዜ ብዛት ተቃዋሚ ድርጅታቸውን ትተው ወደመንግሥት ለመግባት ተወያዩ፡፡
አንደኛው - “እረ ይሄ ድርጅታችን የሚመች አልመሰለኝም፡፡ አደጋው እየበዛ መጣ”
ሁለተኛው - “ዕውነትክን ነው፡፡ እኔም ከዛሬ ነገ ሁሉም ነገር ቅር እያለኝ መሆኑን፤ ልነግርህ
ሳስብ ነበር፡፡”
አንደኛው - “ታዲያ ከዚህ ወጥተን ለምን ወደመንግሥት አንገባም?”
ሁለተኛው - “ይሻለናል”
ተስማሙና ባንድ በሚያውቁት ሰው በኩል ወደ መንግሥት የፖለቲካ መዋቅር ገቡ፡፡ ጠርናፊያቸው አንድ የሚያውቁት ሻምበል ሆነ፡፡
የፖለቲካ ርዕዮተዓለምና አቋም ላይ ተወያዩ፡፡ ተዋወቁ፡፡ ተማማሉ፡፡ የትግሉ አካል ሆኑ፡፡ ንቃታቸው አስተማማኝ ነው፡፡ ቀድሞ በነበሩበት ድርጅት ውስጥ በቂ ንባብ አድርገዋል፡፡
እየነቁ እየተደራጁ ቀጠሉ፡፡ በመካከል ከሁለቱ አንደኛው ወደ ኪዩባ የመሄድ ዕድል ያጋጥመዋል፡፡
ኪውባ ሄዶ፣ ንቃቱን አዳብሮ፣ ትምህርት አበልጽጐ ወደሀገሩ ወደ ኢትዮጵያ ይመለሳል፡፡
ተንሰፍስፎ ያንን የትግል ጓዱን ይፈልገዋል፡፡ ተገናኙ፡፡
“እንዴት ነህ?” አለ ከኩባ የመጣው፡፡
“በጣም ደህና ነኝ፡፡ አንተስ?” አለ አዲሳባ የቆየው፡፡
“ኪውባ በጣም ድንቅ ነበር፡፡ ብዙ ጓዶች አፍርቻለሁ፡፡ የዳበረ ዕውቀት ይዤ መጥቻለሁ ብዬ አምናለሁ” አለው በነቃ ኩራት፡፡
“መልካም፤ በሚገባ ታወራኛለህ!”
“ለመሆኑ ሻምበልስ? ጤናውን እንዴት ነው?”
“ዉ! ሻምበልኮ ታሰረ” አለው እዚህ የቆየው፤ በሀዘንና እንጉርጉሮ ቃና አቀርቅሮ፡፡
ይሄኔ ከኩባ የመጣው በጣም ግራ ገባው፡፡ “እንኲን ታሰረ!” እንዳይል በሳል የማይል ጓዱ ነው፡፡ “ለምን ይታሰራል?” እንዳይል፤ የራሱንም ዕጣ - ፈንታ አያቅም፡፡ ስለዚህ ሲቸግረው፤
“አቤት የአብዮታችን ፍጥነት?!” አለ፤ ጭንቅላቱን በሁለቱ እጆቹ መካከል ቀብሮ፡፡
ጊዜ አለፈና እንደተባለው ሁለቱም ዕጣ - ፈንታቸው እሥር ቤት የሚከትታቸው ሆነና እሥር ቤት ተገናኙ፡፡ ለንፋስ ወጥተው የግል ጨዋታ ሲጨዋወቱ፤
አንደኛው - “እህስ ጓድ፤ አሁንስ የአብዮታችን ፍጥነት ምን ይመስልሃል?”
ሁለተኛው - “አይ ወዳጄ!! አሁንማ አንደኛውን ጄት ሆኖልሃል! ሁላችንንም ጠራርጐን
ገብቷል!” አለ፡፡
* * *
ከሁሉ ነገር በፊት ከመከዳዳት ይሰውረን፡፡ ስለሰው ትተን ስለአብዮታችን ፍጥነት የማናወራበት ጊዜ ይስጠን፡፡ ሁላችንንም ጠራርጐን ገባ የማንባባልበት፤ “ውሃ ሲወስድ አሳስቆን” የማንዘባበትበት ቀና ዘመን ያምጣልን፡፡
የሮጠ ሁሉ እንደማያሸንፍ የሰሞኑ አትሌቲክስ ያስተምረናል፡፡ ድል፤ ሰዓት ጠብቆ ሊቀያየር እንደሚችልም የሰሞኑ አትሌቲክስ ያስተምረናል፡፡ አንዳንዱ ገና ከጅምሩ ሊያቋርጥ እንደሚችል የሰሞኑ አትሌቲክስ ይነግረናል፡፡ ብዙውን የሩጫ ክፍል ሄዶ ሄዶ ማብቂያው ግድም መሸነፍ ሊኖር እንደሚችልም የሰሞኑ አትሌቲክስ አሳይቶናል፡፡ ቢደክሙም፣ ቢዝሉም፣ ውጣ - ውረዱ ከባድ ቢሆንም፤ ሳይታክቱ፤ በጽንዓት ሮጦ እድሉ አምባ ለመድረስ እንደሚቻልም የሰሞኑ አትሌቲክስ ያለጥርጥር አመልክቶናል፡፡
ከሁሉም በላይ ደግሞ ራስን በማዘጋጀት፣ በልበ - ሙሉነትና በብልህነት ጊዜና ቦታን ማወቅ ያለውን ፈትልና ቀስም የሆነ፤ ግንኙነትና ትስስር በአጽንኦት እንድናስተውል ታላቅ ተመክሮን አጐናጽፎናል፡፡ ሩጫ ትንፋሽ እንደሚጠይቅ፤ ትግልም ትንፋሽ ይጠይቃል፡፡ ሩጫ ጉልበት እንደሚፈልግ ትግልም ጉልበት ይፈልጋል፡፡ ሳይዘጋጁ የገቡበት ሩጫ ተሸናፊ እንሚያደርግ፣ ሳይዘጋጁ የገቡበት ትግልም ከተሸናፊነት ጐራ ያስፈርጃል፡፡ ሲሮጡ የታጠቁት ሲሮጡ ይፈታል፤ ይሏል፡፡ ተዘጋጅቶ የሩጫው ሰንበር ላይ ወጥቶም መቼ ማፈትለክ እንዳለብን ካላወቅን፤ የተሻለ ብልጠት ያለው እንደሚቀድመን ሁሉ፤ በትግል ሠፈርም ተዘጋጅቶ ገብቶ ጊዜን ባለማወቅ ሳቢያ፤ ብልጡ ይቀድመናል፡፡ ከሩጫው ሜዳ የተፎካካሪን ብስለትና ጥንካሬ አንዳንዴም ተንኮል ከቁጥር መጣፍ ወሳኝ ነው፡፡ አንዳንዱ ተንከባክቦ የያዘው ጥንካሬ አለው፡፡
ተጋትሮም ተስፈንጥሮም ኬላውን ሰብሮ፣ በጥንካሬው ይዘልቃል፡፡ አንዳንዱ በልምድ ያዳበረው ብስለት አለው፡፡ ስለዚህም የተፎካካሪውን አቅምና በብልህነት የሚጠቀምበትን የጊዜ ሰሌዳ፣ ይመዝናል፡፡ አንዳንዱ የሌሎችን የመሮጫ ረድፍ በመዝጋት፣ ሲመች ጭራሹን በመገፋተር በብልጠትና በተንኮል ይሮጣል፡፡ የባሰበት እስኪነቃበት ዕፅ ይጠቀማል፡፡ እነዚህ የሩጫ ስልቶች የፖለቲካ ስልቶቻችን ተመሳሳይ ገጽታዎች ናቸው፡፡ ሩጫችን ለድል ያበቃን ዘንድ ግብዓቶቹን ሁሉ በአግባቡ ማጤን ዋና ነገር ነው፡፡ “ፈጣን ነው ባቡሩ” እንደምንል ሁሉ፤ “ያልተመለሰው ባቡርን”፤ አልፈን ተርፈንም፤
“እልም አለ ባቡሩ
ወጣት ይዞ በሙሉ” ማለታችንን አንርሳ፡፡
“አወይ መሶሎኒ፤ አወይ መሶሎኒ
ተሰባብሮ ቀረ፣ እንደጃፓን ስኒ” የሚለውም አንድ ሰሞን መዝሙር ነበር፡፡
ይድነቃቸው ተሰማ አንድ ጊዜ ስለሱዳን የእግር ኳስ ቡድን መሻሻል ተጠይቀው፤ “ሱዳን ዘግታ ስትለማመድ ቆይታ፣ ራሷን አጠናክራ፣ ወደፊት መጣች፡፡ እኛ እንደዱሯችን ነው የቆየነው፡፡ በአጠቃላይ አነጋገር “ቆመን ጠበቅናቸው፤ ጥለውን አለፉ!” ብለዋል፡፡ ራስን ማጠናከር ዋና ነገር ነው፡፡
በህመምም፣ በአቅም ማነስም፣ “አውቀው በድፍረት ሳያውቁ በስህተት” ጥፋት ያጠፉም፣ በበላይ ተንኮልና ጥላቻም፣ በፓርቲ ምሥረታም፣ በመተካካትም ሰበብ ሰዎችን ስናገልል ከአጠቃላይ የአገሪቱ ዕጣ - ፈንታ ስዕል አኳያ ማየት ብልህነት ነው፡፡ በተዘበራረቁና በተወሳሰቡ ፖለቲካዊ ምክንያቶች ቂም መያዝ፣ መከፋፈል፣ አንድነትን ማናጋት፣ ወይም መሰነጣጠቅና “የትልቁ አሣ ትንሹን አሣ መዋጥ አባዜ” ማስተናገድ ክፉ ልማድ ነው፡፡ ይህ ልማድ እንዳይደገም “ሃናኔና ሃሪቴ የአምስት ሣንቲም ቅቤ ተካፍለው ሲቀቡ ውለው፣ ወደማታ በአምስት ሣንቲም ጐመን ይጣላሉ” የሚለውን የወላይታ ተረት ማስተዋል ደግ ነው፡፡

Published in ርዕሰ አንቀፅ

(ቁጥር 3)
“አበሻ ፊቱ አይታወቅ፤ ያሸንፍም ይሸነፍም
ፈረንጆቹ ብለው ቢሉም
ለኛ ትታወቂናለሽ፡፡ እፊትሽ ላይ ድል ተጽፏል፡፡
የገጽታሽ ጠይም ብርሃን፣ ልበ ሙሉ ናት ይለናል፡፡
ያልነው አልቀረም ጥሩዬ፤ ነገር የገባት ሰጐን ነሽ፤
ዘንድሮም ተረጋገጠ፣ ክንፍ - ያላት - ሯጭ መሆንሽ፡፡
ብለን ነበር ጐህ ሲቀድ…
“ወትሮም ጀግና ሩቅ ነው ልቡ
ዓለምን እንደጠባብ ቤት፤ በሁለት እግሩ ማሰቡ
ቢሮጥ ነው እንጂ በልቡ
ቢሮጥ ነው እንጂ እንደልቡ
ቢሮጥ ነው እንጂ ከልቡ!!”
ያልነው አልቀረም ጥሩዬ፣ ነገር የገባት ሰጐን ነሽ!
“ንፋስ ሆነሽ ከንፋስ ጋር፣ መሽቀዳደም ሲሆን ዕጣሽ
ከልብ ትርታ ትይዩ፣ ከሥጋት እኩል መሮጥሽ
ከጥላው እንደሚሸሽ ሰው፣ ከባኮው ሾልከሽ መውጣትሽ
ድል - መንገድ በጠዋት ላንቺ፣ የተፃፈ እስኪመስልብሽ
እንደጠይም ብርሃን ንጥቀት፣ ያለኮቴ መመንጠቅሽ”
ያልነው አልቀረም ጥሩዬ፣ ነገር የገባት ሰጐን ነሽ!
ብለን ነበር ጐህ ሲቀድ…
“ባስማት እንዳበሩት ሻማ፣ ተግ ሲል አበሻ ባርቆ
ካጃቢዎች ተፈትልኮ፣ ከባኮው ውስጥ ተመንጭቆ
የቁርጥ ቀን እርምጃ ነው፣ ኮቴው አይሻክርም ደምቆ
ዓለም ምን ያድርግሽ አቦ! ይከተልሽ ቁርጡን አውቆ!
ጥሩዬ ልንገርሽ ዛሬም
“እንኳንስ ተከታይ ሯጭ፣ ተመልካች በዐይኑ አይቀድምሽም፡፡
እግርሽ ካዕምሮሽ ሲፈጥን፣ ያስደነግጣል ጊዜንም፡፡
ሰምበር የበዛው ሜዳ፣ አምስት ሺ ጊዜ ቢዞር
ዥንጉርጉሩ ክብ መንገድ፣ 10ሺ ቀለበት ቢያሥር
ባንቺው እንዝርት - እግር ቀጥኖ፣ እንደድር ተዳውሮ ሲያጥር
ሲጠነጠን እስከድል በር
ይህ እኮ ነው የአገር ኩራት፣ ሁሌም ያሰቡበት ማደር!
ጥሩዬ ልንገርሽ ዛሬም፣ አንቺም ንገሪያት ላገርሽ
“ሩጫችን የወል ጣር ነው፣ ድልም በደቦ ነው ሚያምረው
እርሻ በጅጊ ነው እሚሠምር፤ ጓዛችን አንድ ልብ ነው
ጉዟችን የአገር ልማድ ነው፤
ተናቦ ተቧድኖ መርታት፣ አንድነት ባህላችን ነው!
ዛሬም ንገሪያት ለአገርሽ፣ የሩቅ የሀቅ ወርቅ አንጥረሽ
ድልሽን “እንደድመት ግልገል፣ በጥርስሽ ጫፍ አንጠልጥለሽ”
በዓለም ሰማይ ከዓለም በላይ፣ የባንዲራ ዳስሽን ጥለሽ
ሜዳልሽን፣ ባገርሽ ክብር ውስጥ፣ እንዳራስ ፈገግታ አንጣለሽ
ከሠገነት በላይ ሰንደቅ፣ ከሰው በላይ ድልሽን ሰቅለሽ
የባንዲራችን ነበልባል፣ አየሩን ሸፍኖባቸው
የዓለም ባንድሮች ከመሬት፣ ሰማይ ማየት አቃታቸው፡፡
ጥሩዬ በእኔ ሞት ብለን፣ ገና በጧት ቃል አንቅተን
በገዛ እጅ አካል ዳብሶ፣ ተዘጋጅቶ መንደርደርን
ከቶም ከመሯሯጥ መሮጥ፣ ሺ ጊዜ መብለጥ መላቁን
በትዕግስት መነሳትን፣ በትዕግስት ዳር መድረስን
በትንፋሽ ጉልበት መግዛትን፣ በትንፋሽ ኬላ መስበርን
ዛሬም በእኔ ሞት ጥሩዬ፣ መላውን ለአገር ንገሪ
አንቺ አገር ነሽ፣ የአገር ጠሪ
ጊዜ አይተሽ የምትሰግሪ
ጊዜ አይተሽ የምትበርሪ
አንቺ ጠይም የሰው ጨረር፣ ጠይም ኮከብ ታሪክ ሰሪ
ነገር የገባት ሰጐን ነሽ፣ ጥሩዬ በእኔ ሞት ኩሪ!
ይቻላል በያት አገርሽን፣ አርፎ ተነስቶ መሮጥ
ይቻላል በያት አገርሽን፣ ቦታ ማየት፣ ጊዜ መምረጥ
ተፎካካሪን እያዩ፣ በርቀት፣ በስላች ማምለጥ
ዛሬም በሥራ ንገሪን፣ ላገር ነውና ድካምሽ
ያልነው አልቀረም ጥሩዬ፣ ነገር የገባት ሰጐን ነሽ!!
ነሐሴ 9/2005
(ለጥሩዬ፣ ለኢትዮጵያ ህዝብና ለልደቴ)

Published in የግጥም ጥግ

“ተቃዋሚዎች ከአክራሪዎች ጋር የፈፀሙት ያልተቀደሠ ጋብቻ ለህዝቡ ስጋት ሆኗል” - አቶ ሽመልስ ከማል (ሚ/ዴኤታ)

አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ፣ በመቀሌና በወላይታ ሶዶ ከተሞች ሠላማዊ ሠልፍና ህዝባዊ ስብሠባ ለማካሄድ የነበረው እቅድ በተለያዩ ጫናዎች መጨናገፉን የፓርቲው ሊቀ መንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ገለፁ። 

የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት ሚኒስትር ዲኤታ አቶ ሽመልስ ከማል በበኩላቸው፤ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የጠበቁትን ያህል የህዝብ ድጋፍ ሲያጡ የራሳቸውን ድክመት ለመሸፈን መንግስትን ይወነጅላሉ ብለዋል፡፡
አንድነት ፓርቲ በ16 ከተሞች ሠላማዊ ሠልፍና ህዝባዊ ስብሠባ ለማካሄድ እቅድ አዘጋጅቶ ተግባራዊ እያደረገ መሆኑን የተናገሩት ዶ/ር ነጋሶ፤ በየከተማው የፓርቲውን እንቅስቃሴ ለማደናቀፍ ሙከራዎች አጋጥመውናል ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ፣ ከመቀሌ እና ከወላይታ ሶዶ በስተቀር በሌሎች ከተሞች ሠላማዊ ሠልፎችና ህዝባዊ ስብሠባዎችን በስኬት ለማከናወን ችለናል ብለዋል፡፡ ሐምሌ 28 ቀን በመቀሌ ሊካሄድ የነበረው ሠላማዊ ሠልፍ የተጨናገፈው ለቅስቀሣ የምንጠቀምበት መኪና በመታገቱ ነው የሚሉት የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ዳንኤል ተፈራ፤ በከተማዋ ያሉ የፓርቲያችን አስተባባሪዎች በመታሠራቸውም እቅዳችን ሳይሳካ ቀርቷል ብለዋል።

“ሠልፍ ማካሄድ አትችሉም” የሚል ግልጽ ክልከላ ባያጋጥመንም፣ በተለያዩ መሰናክሎች ሳቢያ ፓርቲው በገዛ ፈቃዱ ሠልፉን መሠረዙን አቶ ዳንኤል ገልፀዋል፡፡ በወላይታ ሶዶ ከተማም በዚያው እለት ህዝባዊ ስብሠባ ለማካሄድ ታስቦ እንደነበር አስታውሰው፣ ስብሠባው የሚካሄድበትን አዳራሽ ከፍተን ለመግባት አልቻልንም የሚሉት አቶ ዳንኤል፤ ቁልፍ ጠፍቶ የስብሠባው ሠአት ካለፈ በኋላ ነው የተገኘው ብለዋል፡፡ የታሠበውን ያህል ተሣታፊ ባለመገኘቱም ስብሠባው ስኬታማ አልሆነም ሲሉም ተናግረዋል፡፡
“አንድነት በተለያዩ ከተሞች ሠላማዊ ሠልፍ እና ህዝባዊ ስብሠባ በማድረጉ ኢህአዴግ ግራ ተጋብቷል” የሚሉት ዶ/ር ነጋሶ፤ በአርባምንጭና በወላይታ ሶዶ የቅስቀሣ መኪኖች እንዳይንቀሣቀሡ ጐማ በማስተንፈስ እንቅፋት ለመፍጠር ተሞክሯል ብለዋል፡፡ በባህርዳርም፣ በሠልፉ ተሣታፊ የነበሩ ባጃጆች ታርጋ ተፈትቶ እንደተወሰደባቸው ዶ/ር ነጋሶ ገልፀዋል፡፡ በተቃዋሚ ፓርቲዎች እየተካሄዱ ባሉት ሠላማዊ ሠልፎችና ህዝባዊ ስብሠባዎች ዙሪያ የመንግስትን አቋም እንዲገልፁልን የጠየቅናቸው የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ሚኒስትር ዲኤታ አቶ ሽመልስ ከማል፤ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በህገመንግስት የተከበረላቸውን መብት እያጣጣሙ መሆናቸውን የሚያመለክት ነው ብለዋል፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የሚመሠረቱበት አላማ ለመቃወምና ሃሣባቸውን በሠላማዊ ሠልፍ ወይም በህዝባዊ ስብሠባ ለመግለፅ መሆኑን አቶ ሽመልስ ጠቅሰው፣ ይህም በህገመንግስት የተፈቀደላቸው መብት ነው ብለዋል፡፡

ነገር ግን አንዳንድ ተቃዋሚዎች ከአክራሪ ሃይሎች ጋር የፈጠሩት “ያልተቀደሠ ጋብቻ” ለህዝቡ ስጋት መሆኑን የተናገሩት አቶ ሽመልስ፤ መንግስትም በዚህ ሁኔታ ህገ መንግስቱ ሲጣስ ከዳር ቆሞ አይመለከትም ብለዋል፡፡ ተቃዋሚዎች በሰልፍና በስብሰባ ጥሪ የጠበቁትን ያህል ሠው ሣይወጣላቸው ሲቀር፣ የራሳቸውን ድክመት ለመሸፋፈን መንግስትን ተጠያቂ ለማድረግ ይሞክራሉ ያሉት አቶ ሽመልስ፤ መንግስት ጫና በማድረጉ ሠው ሊወጣልን አልቻለም የሚለው የተቃዋሚዎች ስሞታ መሠረት የሌለው ውንጀላ ነው ብለዋል፡፡

Published in ዜና
Saturday, 17 August 2013 11:21

የአገር ሰምና ወርቅ 

ልለምንህ ጣና - ልማጠንህ ዓባይ - አዋሽ እሺ በለኝ
አገሬ ተድራ - አገር ጠርቻለሁ - የአገር ድግስ አለኝ፤
አገሩን የዳረ - አገር ህዝብ የጠራ
ለአገር የጠመቀ - ለአገር የደገሰ፣
መሬቱ እንጀራው ነው - ሀይቁም ወይንጠጁ
መች ይጨንቀውና - ደረሰ አልደረሰ፤
ይኸው አገር መጣ!
ይኸው አገር ወጣ!
አገር ድግስ በይ - አገር ላይ የወጣ - አገር ሊያይ የመጣ
ብትታየው ጊዜ - አገር ሙሽራዬ - ከአገር ሁሉ በልጣ
አገር ልቡ ቆመ - አገር ማድነቂያ አጣ - አገር አቅም አጣ፡፡
ይኸው ይቺውልህ፤
በአገር ፍቅር ቬሎ - በአገር ሰረገላ
አገር ስትመዘን - በሰው ተመስላ
ይህን ታህላለች
ይህን ትመስላለች
በል ሀቅ እንፈልቅቅ - ከሯጭ ህብረ - ቀለም
በአትሌት ሰምና ወርቅ - በ‹‹ሀገር›› ቀልድ የለም!!
ለዚያም ነው ጥሩዬ
አገር በልቧ አዝላ - በአገር ተውባ
በአገራት ሙሽሮች - በአገራት ተከባ
በአገር አደባባይ - አገር ስታገባ
አገር ወዲያ ጥላ - ወደ አገር ስትገባ
አገር ምድሩ ያለው - ጉሮዬ ወሸባ!!
ነው እንጅ ነውና!!
‹‹ጥሩ›› አገር ብትሆን ነው - አገርን ያከለች - አገር የተሰጠች
ከአገር ተፎካክራ - አገር ያስከተለች - አገር የበለጠች!!
ይኸው ነው ቀለሙ - ይኸው ነው እውነቱ
እሷ ስታሸንፍ - እኛ ሁላችንም - የጨፈርንበቱ!!
ስማ ጋዜጠኛ፤
ይኸውልህ እውነት - የሀቅ ህብረ - ቀለም
በጥሩነሽ አገር - ስለ አገር ቀልድ የለም፡፡
ካላመንክ ጠይቃት - ከአንደበቷ ስማ
እንዲህ ትልሃለች - አገር አስቀድማ...
‹‹ለሌላ አገር አትሌት - እንኳን ሜዳሊያ - መጨረስም ድል ነው
ለኔ አገር ህዝብ ግን - ብር ሽንፈት ሲሆን - ነሀስም ውራ ነው፤
በቃ በኔ ሀገር - ድል ነው እሚባለው
ወርቁን ከነክብሩ - ያስገኘህ ጊዜ ነው!!››
ይህ ነው ሰምና ወርቅ - በጥሩነሽ አገር - የአገር ህብረ - ቀለም
ወርቅ ለለመደ - ነሀስ ግድ አይሰጥም - ብርም ድል አይደለም፡፡
ነሐሴ 5 - 2005 ዓ.ም
(ለአትሌት ጥሩነሽ ዲባባ የሞስኮ ድል)

Published in የግጥም ጥግ


ፓርቲው በአባላቱ ላይ እየደረሰ ያለው እንግልት እንዲቆም ጠይቋል

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፍልስፍና መምህር የሆኑት ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፤ ነገ ረፋድ ላይ በሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት በአገሪቱ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ትምህርት ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ 
“እኔ ልናገር የምችለው በፍልስፍና ጉዳዮች ዙሪያ ነው” ያሉት ምሁሩ፤ በህግ በሰብአዊ መብት ፣ በፖለቲካ፣ በትምህርትና በአገሪቱ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ትምህርት እንደሚሰጡ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
“እሁድ ረፋድ ላይ በማቀርበው ትምህርት ገዢው ፓርቲ ብቻ ሳይሆን የተቃውሞ ጐራውም አካባቢም ሸንቆጥ ይደረጋል” ያሉት ዶ/ር ዳኛቸው፤ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ተገኝቶ በአገሪቱ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ሀሣብ ማካፈል ይችላል ብለዋል፡፡ ሠማያዊ ፓርቲ በተለያዩ ጊዜያት ምሁራንን እየጋበዘ በአገሪቱ ወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳይ ላይ ለማህበረሠቡ ትምህርት እንዲሰጡ የሚያደርግ ሲሆን ዶ/ር ዳኛቸው ከዚህ ቀደም ተደጋጋሚ ግብዣ ቀርቦላቸው በስራ ብዛት ሳይመቻቸው እንደቅ አስታውሰው፤ ለነገው ፕሮግራም ግን በዝግጅት ላይ እንደሆኑም ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል ሰማያዊ ፓርቲ ትላንትና ባወጣው መግለጫ፤ በአባላቱ ላይ እየደረሰ ያለው የመብት ረገጣና እንግልት እንዲቆምመንግስትን ጠይቋል፡፡
“የሀገራችን የመንግስት አወቃቀር ዋና መሠረቱ ዘርና ቀለም ነው” ያለው ፓርቲው፤ ዜጐች በመልካም አስተዳደር፣ በማንነትና በመሰል ችግሮች ዙሪያ ጥያቄና እሮሮ በማሰማታቸው ከፍተኛ እስርና እንግልት እየደረሰባቸው በመሆኑ፣ ድርጊቱ በአስቸኳይ እንዲቆም እጠይቃለሁ ብሏል በመግለጫው፡፡ ፓርቲው ግንቦት 25 ቀን 2005 ዓ.ም ባካሄደው ሰላማዊ የተቃውም ሰልፍ ካነሳቸው ጥያቄዎች አንዱ የመልካም አስተዳደር እጦት እንደነበር ያስታወሰው መግለጫው፤ መንግስት የህዝቡን ጥያቄ ከመመለስ ይልቅ ህገ-ወጥ የመብት ረገጣውን መቀጠሉ በጋሞጐፋ ዞን በቁጫ ወረዳ ህዝብ ላይ የሚደርሰው ተደጋጋሚ በደል ማሳያ ነው ብሏል፡፡ የቁጫ ወረዳ ነዋሪዎችም የመንግስት ጫና ሳይበግራቸው ሰላማዊ ትግላቸውን እንዲቀጥሉ ያሳሰበው ፓርቲው፤ መንግስት በወረዳው ነዋሪዎች ላይ የሚያደርሠውን እስርና እንግልት በአስቸኳይ እንዲያቆም ሲል አሳስቧል፡፡

Published in ዜና

በሶስት ቋንቋዎች የፓርቲው ልሳኖች ይዘጋጃሉ

አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ የራሱን ማተሚያ ቤት ለመክፈት ባለፉት ሶስት ወራት በአገር ውስጥና በውጭ ባከናወነው የገቢ ማሰባሰቢያ ጥረት በቂ ገንዘብ ማግኘቱን በመግለጽ የማተሚያ ማሽን የግዢ ጨረታ አወጣ።
በፓርቲው ሲዘጋጅ የነበረው “ፍኖተ ነፃነት” ጋዜጣ በማተሚያ ቤት እጦት እንደተቋረጠ የገለፁት የፓርቲው አመራር አባል፣ ማተሚያ ማሽን ተገዝቶ ስራ ሲጀምር “ፍኖተ ነፃነት”ም ለአንባቢያን ትደርሳለች ብለዋል፡፡ ከጋዜጣው በተጨማሪ በትግርኛና በኦሮሚኛ ቋንቋዎች የሚዘጋጁ ጋዜጦችና ሌሎች ህትመቶችንም እንደሚሰራ ፓርቲው ጠቅሶ፣ ፓርቲዎች በንግድ ስራ ውስጥ መግባት ስለማይችሉ ለግል ጋዜጦች የህትመት አገልግሎት አንሰጥም ብሏል። የሀገር ውስጥ አቅራቢዎች በጋዜጣ ላይ በወጣ የጨረታ ማስታወቂያ በቀረበው ዝርዝር መረጃ መሠረት መሳተፍ እንደሚችሉ የተናጋሩት የፓርቲው ተወካይ፤ ማሽኑን ከሀገር ውስጥ መግዛት ያስፈለገበት ምክንያት ከውጭ ተገዝቶ ሲገባ ያለውን ረጅም ጊዜ ለመቀነስና ማሽኑን በተመጣጣኝ ዋጋ ለመግዛት እንደሆነ ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በተለያዩ ህገ-ወጥ የከተማ ንግዶች ላይ እርምጃ ለመውሰድ ማቀዱን ገለፀ፡፡ በከተማዋ በቀላል ባቡር እና በመንገድ ግንባታ ምክንያት ህዝቡ በትራንስፖርት ችግር እየተሰቃየ በመሆኑ የጐዳናና የበረንዳ ንግድ ቅድሚያ እልባት ያገናኛሉ ተብሏል፡፡
ከትላንት በስቲያ በከተማ አስተዳደሩ ካቢኔ አዳራሽ የመስተዳድሩ የንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ሀላፊ አቶ ሺሰማ ገ/ስላሴ፣ የአዲስ አበባ ከተማ ደንብ ማስከበር ስራ አስኪያጅ ረዳት ኮሚሽነር ሀይሌ አማረና የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ዋና ስራ አስፈፃሚ ኢ/ር ፈቃደ ሀይሌ በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ በርካታ ህገ-ወጥ ድርጊቶች በከተማዋ የተስፋፉ ቢሆንም፣ አሁን ባለው ሁኔታ በህገ-ወጥ ንግድ የተያዙ የከተማዋ ዋና ዋና ጎዳናዎች፣ በህገ-ወጥ ግንባታና በሼድ የተያዙ መንገዶች እንዲሁም በረንዳዎች መለቀቅ እንዳለባቸው ተገልጿል፡፡

እስካሁን በተካሄው ጥናትም ዘጠኝ ሺህ የበረንዳ ነጋዴዎችና ስምንት ሺህ የጐዳና ላይ ነጋዴዎች ሲነግዱ መመዝገባቸውን ሀላፊዎቹ ገልፀዋል፡፡
በገበያ ጣልቃ ገብነት፣ በት/ቤቶች ዙሪያ በሚደረጉ አዋኪ ንግዶች፣ በጋራ መኖሪያ ቤቶች ዙሪያ በህጋዊ ንግድ ፈቃድ ስም ህገ-ወጥ ንግድ የሚካሄዱና ለትውልድ ስነ-ምግባር እንቅፋት የሆኑ ንግዶችን ለማስቆም እስካሁን ተስፋ ሰጪ እርምጃዎች እንደተወሰዱ የተገለፀ ሲሆን፣ በአሁኑ ሰዓት ግን አንገብጋቢውና ለከተማው ነዋሪ ፈተና የሆነው የበረንዳና የጐዳና ላይ ንግድ ቅድሚያ ተሰጥቷቸው የሚሰሩ እንደሆኑ ተገልጿል፡፡

በተለይም ከመገናኛ ኡራኤል፣ ከኡራኤል ሜክሲኮና ፒያሳ አካባቢ ያለው የበረንዳና የጐዳና ላይ ንግዶች ቅድሚያ ያገኛሉ፡፡
ይህ ማለት የጐዳና ነጋዴዎች አይስሩ ማለት እንዳልሆነ ሀላፊዎቹ ገልፀው፣ ቢቻል በተለያየ መንገድ ተደራጅተው ቋሚ ተጠቃሚ የሚሆኑበትን መንገድ መያዝ፣ አይ እኔ የማውቀው ስራ ይሄ ብቻ ነው ካሉም በተፈቀደ ቦታ፣ በተፈቀደ ሰዓትና በተፈቀደ ቀን መስራት እንደሚኖርባቸው ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ ደንብ ማስከበር ስራ አስኪያጅ ረዳት ኮሚሽነር ሀይሌ አማረ በበኩላቸው፤ በ2002 ቢፒአር ሲሰራ ደንብ ማስከበር የተባለው አካል አስፈላጊ አይደለም ተብሎ ደንቦችን ሴክተር መስሪያ ቤቶች እንዲያስከብሩ የተወሠነ መሆኑን ገልፀው፣ በሌላ ጥናት ግን ሴክተር መስሪያ ቤቶች ደንብ ማስከበሩን እንዳልሸፈኑት መረጋገጡን ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም ደንብ ማስከበሩ በአዲስ መልክ መቋቋሙንና ለዚህም ስራ የሚሆኑ ከ2000 በላይ ሰዎች በጦላይ ማሰልጠኛ ለሁለት ወራት ስልጠና ወስደው ከግንቦት 1 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ተግባር የተገባ መሆኑን የገለፁት ረዳት ኮሚሽነሩ፣ ህገ-ወጥ ነጋዴዎች በተደጋጋሚ በሚሰጣቸው ትምህርትና ከህገ-ወጥነታቸው ካልታቀቡ ደንብ ማስከበሩ ባለው ጠንካራ የህግ ማዕቀፍ ለየትኛውም ሴክተር መስሪያ ቤት ጉዳዩን ሳያቀርብ እርምጃ የመውሰድ ስልጣን እንዳለው ገልፀዋል፡፡ ደንብ ማስከበሩ ከንግድ ቢሮው ጋር በትብብር እንደሚሰራም ሃላፊው ተናግረዋል፡፡
በህገ-ወጥ መንገድ የተሰማሩ የጐዳና ላይ ነጋዴዎች የስራ ቦታን በተመለከተ፣ በየወረዳቸው ማመልከት እንደሚችሉም ተገልጿል፡፡
የአገራችን የንግድ ስርዓት ከየት እንደመጣ ይታወቃል ያሉት ሀላፊዎቹ፤ ይህንን ህገ-ወጥነት ለማስቀረት ከቅጣትና ከእርምጃ ከመጀመር በማስገንዘብና በማስተማር መለወጥ ይሻላል በሚል የተለያዩ የምክክር መድረኮችን አመቻችተን እየሰራን ነው ብለዋል፡፡
አዲስ አበባ ውስጥ ነጋዴ የሆነና ያልሆነውን ለመለየት ጥናት የተደረገ ሲሆን መረጃውም በአሻራ ላይ የተመሰረተ እንደሆነ አቶ ሺሰማ ተናግረዋል፡፡ አዲስ አበባ ውሰጥ 230ሺህ ነጋዴ አለ ሲባል የነበረ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 139ሺህ ብቻ ወደ ህጋዊ ስርዓቱ ገብቶ ቀሪው መስፈርት ባለማሟላት አየር ላይ ቀርቷል ተብሏል፡፡
ያለ ንግድ ፈቃድ ሲነግዱ የነበሩትን የቤት ለቤት አሰሳ በማድረግ፣ 86ሺህ ያህሉን ወደ ስርዓቱ ማስገባት ተችሏል ብለዋል፡፡ ነጋዴው በመረጃ ላይ የተደገፈ ስራ እንዲሠራ የመረጃ ኔትወርክ ከወረዳ እስከ ፌደራል መዘርጋቱም ተገልጿል፡፡

Published in ዜና

ለተጨማሪ ህክምና ዛሬ ወደ ኬኒያ ይሄዳል
“አንድ ቃል” በተሰኘው የመጀመሪያ አልበሙ ተወዳጅነትንና እውቅናን ያተረፈው ድምፃዊ ኢዮብ መኮንን፣ “ስትሮክ” ተብሎ በሚታወቀው ህመም ቅዱስ ገብርኤል ሆስፒታል የገባ ሲሆን ለተጨማሪ ህክምና ወደ ኬንያ ይሄዳል ተብሏል፡፡ በጅጅጋ ከተማ ተወልዶ ያደገው የ38 ዓመቱ ድምፃዊው፤ በቅዱስ ገብርኤል ሆስፒታል ኢንቴንሲቭ ኬር ዩኒት (ICU) ውስጥ በህክምና ላይ እንደሚገኝ ባለቤቱ ወ/ሮ ቲና ተአረ ተናግራለች፡፡ 
ትላንትና ረፋዱ ላይ በሆስፒታሉ ያገኘናት ባለቤቱ ወ/ሮ ቲና፣ ማክሰኞ ጠዋት የእህቱን ልጅ ት/ቤት አድርሶ ከተመለሰ በኋላ የቤቱን መጥሪያ እንደተጫነ መውደቁንና በድንጋጤ ወደ ሆስፒታል ይዘውት እንደመጡ ገልፃለች፡፡
“ከዚህ በፊት የከፋ ህመም አጋጥሞት አያውቅም፣ ባለፈው እሁድም ኮሌስትሮልን ጨምሮ ጠቅላላ የጤና ምርመራ አድርጓል” ብላለች፡፡ ኢዮብ ለተጨማሪ ህክምና ዛሬ ወደ ኬኒያ እንደሚሄድም ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ ይሁን እንጂ ከመጀመሪያው አሁን የጤና መሻሻል እንዳለው ባለቤቱ ተናግራለች፡፡

Published in ዜና

በሳምንት አንድ ቀን ውሃ ማግኘት ብርቅ የሆነባቸው ሰፈሮች፣ በውሃ እጦት አካባቢያቸውን በመጥፎ ጠረን የሚበክሉ የኮንዶሚኒየም መኖሪያዎች፣ ለተደጋጋሚ አቤቱታ ምላሽ ሳያገኙ በርካታ ወራት እየተቆጠሩ የሚማረሩ ነዋሪዎች የአዲስ አበባ የዘመኑ ገጽታ ሆነዋል፡፡
በቂ ውሃ ስለሌለ በራሽን ለማከፋፈል እየሞከረ መሆኑን የሚልፀው የውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን በበኩሉ፤ የኤሌክትሪክ መቆራረጥና የአንዳንድ ሰራተኞች እንዝህላልነት፣ ለመንገድ ግንባታ የሚቆፈሩ ቧንቧዎች እንዲሁም በከንቱ የሚባክን ውሃ መብዛቱ የውሃ እጥረትን እንዳባባሱ ይናገራል፡፡
የአገሪቱ እንዲሁም የአህጉሪቱ መዲና በሆነችው ከተማ፣ ለዚያውም በሰለጠነ ዘመን በርካታ ነዋሪዎች የዝናብ ውሃን ደቅኖ ለማጠራቀም ሲሯሯጡና በጀሪካን ተሸክመው ውሃ ሲያመላልሱና የፎቅ ደረጃዎችን ለመውጣት ሲውተረተሩ ማየት የተለመደ ሆኗል፡፡
በገርጂ፣ አየር ጤና፣ ጀሞ፣ እንቁላል ፋብሪካ፣ አዲሱ ገበያ፣ እንዲሁም በየአቅጣጫው የተገነቡ ኮንዶሚኒየሞችን ጨምሮ በርካታ የከተማዋ ሰፈሮች፣ በውሃ እጥረት የተቸገሩ ነዋሪዎች “አወይ ስልጣኔ” በማለት መላ እንደጠፋባቸው ይገልፃሉ፡፡
የፉሪ አካባቢ ነዋሪ ወ/ሮ አልማዝ ሞገስ፣ ቀድሞም ቢሆን በሁለት በሶስት ቀን ነበር ውሃ የምናገኘው ይላሉ፡፡ አሁን ግን ብሶበታል፣ ይሄውና በሰፈሩ ውሃ ካገኘን ከሳምንት በላይ ሆኖናል የሚሉት ወ/ሮ አልማዝ፤ ውሃ የምናገኘው ጀሪካን ተሸክመን ሰፈር አቆራርጠን ነው ብለዋል፡፡
ብዙ ጊዜ አቤቱታ አቅርበን ደከመን፤ ምንም መልስ አላገኘንም ብለዋል - ወ/ሮ አልማዝ፡፡
በጀሞ ቁጥር 1 መኖር ከጀመረች ሁለት አመት የሆናት ሰናይት ፈቃደ በበኩሏ፣ የውሃ ችግር የጠናብኝ ዛሬና ትላንት አይደለም፣ በጣም ቆይቷል ትላለች፡፡ ድሮ ድሮ ሌሊት ላይ ብቅ ይል የነበረው ውሃ፤ ዛሬ ሽታውም የለም የምትለው ሰናይት፣ የኮንዶሚኒየም ቤት ያለ ውሃ የስቃይ ቤት ማለት ነው ብላለች፡፡ የመጀመሪያ ፎቅ ነዋሪዎች የዝናብ ውሃ ደቅነው ለማጠራቀም ይሞክራሉ፣ ሁለተኛና ሦስተኛ ፎቅ ግን አይሞከርም፡፡ ቧንቧ በየቤታችን አለ፤ ውሃ የምናመጣው ግን እንደ ጥንቱ የገጠር አኗኗር ነው የምትለው ሰናይት፤ ለውሃና ፍሳሽ አመልክተናል፡፡ ውሃውን ወደ ላይ ለመሳብ የፓምፕ ሃይል ስለሚያስፈልግ ነው ይሉናል፤ ይህንን እንደ በቂ ምላሽ ይቆጥሩታል በማለት ግራ መጋባቷን ትገልፃለች፡፡
ጀሞ ብቻ አይደለም፡፡ የጐሮ ነዋሪ ናርዶስ አስማረ አንድ ቀን ውሃ ከመጣ ለሁለትና ለሶስት ቀን ይጠፋል፤ ቅዳሜና እሁድ ውሃ ያገኘንበት ጊዜ የለም ትላለች፡፡ በየሳምንቱ አቤቱታ ስናቀርብ የምናገኘው ምላሽ ሁልጊዜ ተመሳሳይ ነው የምትለው ናርዶስ፤ አሁን ይስተካከላል ይሉናል፤ ግን ተስተካክሎ አያውቅም ትላለች፡፡
ውሃ የሚጠፋበትን ቀን ዘርዝሮ ከመናገር ይልቅ ውሃ የሚመጣበትን ቀን መናገር ይቀላል የሚለው የአዲሱ ገበያ ነዋሪ ልዩነህ አያሌው፤ ውሃ ይግባልን ብንል ይሻላል፤ በሳምንት አንዴ ውሃ ከመጣ ፌሽታ ነው፤ ብርቅ ይሆንብናል ሲል ይናገራል፡፡
አዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ አገልግሎት የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሃላፊ ወ/ሮ እፀገነት ተስፋ ምላሽ ሲሰጡ፤ በአዲስ አበባ የውሃ ችግር አለ በማለት ነው የሚጀምሩት፡፡ ዋናው ምክንያት የውሃ እጥረት ነው የሚሉት ወ/ሮ እፀገነት፤ ከነእጥረቱም ቢሆን ውሃውን ለህብረተሰቡ ለማድረስ ደግሞ የተለያዩ መሰናክሎች እንደሚገጥሙ ገልፀዋል፡፡
ኤሌክትሪክ ሲቋረጥ ከፍታ ቦታ ላይ ለሚገኙ ነዋሪዎች በፓምፕ ውሃ ማድረስ አንችልም ይላሉ፡፡ ሌላው ችግር በራሳችን ሰራተኞች የሚፈጠር ነው የሚሉት ሃላፊዋ፣ የውሃ ቧንቧ ተበላሽቷል ተብሎ ሲነገራቸው አንዳንድ ሰራተኞች ብልሽቱን እንደመጠገን ውሃውን ዘግተውት ይመጣሉ ብለዋል፡፡ በመንገድ ስራና የተለያዩ ግንባታዎች የውሃ ቧንቧ እንደሚሰበር ሲያስረዱ፣ ለምሳሌ በሃያ ሁለት አካባቢ፣ በመንገድ ግንባታ ምክንያት ዋናው የውሃ ቧንቧ በመቋረጡ አሁን በተዘረጋ ጊዜያዊ ቧንቧ የምናቀርበው ውሃ በአስር እጥፍ ያነሰ ነው ብለዋል፡፡ በዚያ ላይ ለከተማዋ ከሚቀርበው ጠቅላላ የውሃ መጠን ውስጥ ከአንድ ሦስተኛ የሚበልጠው በከንቱ ይባክናል ብለዋል ሃላፊዋ፡፡ የከተማዋን የውሃ ችግር ለማቃለል 11 የውሃ ጉድጓዶች ተቆፍረው 10 ስራ መጀመራቸውን ወ/ሮ እፀገነት ጠቅሰው፤ ከለገዳዲ ይቀርብ የነበረውን 165ሺ ሜትር ኪዩብ ውሃ፣ ወደ 195ሺ ሜትር ኪዩብ ለማሳደግ እየሰራን ነን ብለዋል፡፡ በገርጂ አካባቢ በ2.5 ቢሊዮን ብር ወጪ 100ሺ ሜትር ኪዩብ ውሃ ለማቅረብ ግንባታው በ2006 ይጀመራል፤ በሁለት እና ሦስት አመት ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ችግሩ እንደሚፈታ እርግጠኛ ነኝ ያሉት ሃላፊዋ፣ ነዋሪዎች ቅሬታቸውን በ906 በመደወል እንዲሁም በአመት 3 ጊዜ በምናካሂደው የደንበኞች ፎረም ማሰማት ይችላሉ ብለዋል፡፡

Published in ዜና
Page 10 of 17