የአቃቢያን ህግ ዳይሬክተር የነበሩት አቶ እሸቱ ወ/ሠማያትን ጨምሮ 10 ተጠርጣሪዎች በዋስ ተለቀዋል፡፡
የተጠርጣሪ ባለሃብት ኩባንያዎች አስተዳደር እስከ መስከረም ባለበት እንዲቀጥል ብይን ተሰጠ፡፡

የፌደራሉ የስነምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን መርመሪ ቡድን ከኦዲት ስራ በስተቀር የ6 መዝገቦች ምርመራ አጠናቆ በማስረከቡ አቃቤ ህግ ክስ የመመስረቻ የ15 ቀን ጊዜ ተጠርጣሪዎቹ መካከል በኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን የአቃቢያን ህግ ዳይሬክተር የነበሩትን አቶ እሸቱ ወ/ሰማያትን ጨምሮ አስር ተጠርጣሪዎች በዋስ ተለቀዋል፡፡
የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 2ኛ ወንጀል ችሎት በትናንት ከሰአት በኋላ ውሎው የገቢዎችና ጉምሩክ ዳሬክተር አቶ መላኩ ፈንታን እና ምክትላቸው አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስን ጨምሮ፣ በስድስት መዝገቦች የ47 ተጠርጣሪዎችን ጉዳይ ተመልክቷል፡፡
የኮሚሽኑ መርማሪ ቡድን ፍ/ቤቱ በሰጠው ጊዜ ውስጥ ከኦዲት ምርመራው በቀር ሁሉንም የምርመራ ስራዎች ማጠናቀቁን በመግለጽ፣ ተጠርጣሪዎች ከእንግዲህ ጉዳያቸውን ማረሚያ ቤት ሆነው እንዲከታተሉ ፍ/ቤቱን ጠይቋል፡፡ ከኦዲት ምርመራው ጋር በተያያዘ፣ የኢንተር ኮንቲኔታል ባለቤት አቶ ስማቸው ከበደ፣ የኬኬ ባለቤት አቶ ከተማ ከበደ፣ የነፃ እና ባሰፋ ትሬዲንግ ኩባንያ ባለቤት አቶ ነጋ ገ/እግዚአብሔር እንዲሁም ባለሃብቱ አቶ ምህረተ አብ አብርሃ እዚያው ባሉበት የፖሊስ ማረፊያ ቤት እንዲቆይ መርማሪ ቡድኑ ጠይቋል፡፡
በሌላ በኩል አቶ እሸቱ ወ/ሰማያት እና ትዕግስት አለማየሁ፣ በእነ አቶ ገ/ዋህድ መዝገብ ተካተው የነበሩት አቶ ተወልደ ብስራት፣ አቶ ሙሉቀን ተስፋዬ፣ አቶ ዳኜ ስንሻው እና ወ/ሮ ፍሬ ህይወት ጌታቸው፣ አቶ ባህሩ አብርሃ እንዲሁም አቶ ስዩም ለይኩን፣ አቶ ሃይለማርያም አሰፋ እና ወ/ሮ አልማዝ ከበደ በዋስ መለቀቃቸው ታውቋል፡፡
ከኦዲት ስራ በስተቀር ምርመራው ተጠናቅቆ ከመርማሪ ቡድኑ መዝገቦቹን እንደተረከበ ያረጋገጠው የኮሚሽኑ አቃቢ ህግ፣ ተጠርጣሪዎቹ ባሉበት ሆነው ክስ የመመስረቻ የ15 ቀን ጊዜ እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ በተጠርጣሪዎቹ የዋስትና መብት ላይ አስተያየቱን እንዲያቀርብ የተጠየቀው አቃቢ ህግ፣ የተፈፀመው ወንጀል ከባድ የሙስና ወንጀል በመሆኑና ክስ ሲመሰረት የሚጠቀሰው አንቀጽም ከ10 አመት በላይ ሊያስቀጣ የሚችል ስለሆነ የዋስትና መብት የሚያስከለክል ነው ብሏል፡፡
የተጠርጣሪ ጠበቆች በበኩላቸው የተለያዩ የህግ መከራከሪያ አቅርበው የደንበኞቻቸው የዋስትና መብት ተጠብቆ ጉዳያቸውን በውጭ እንዲከታተሉ ይደረግ ዘንድ ጠይቀዋል፡፡ የግራ ቀኙን ክርክር ሲያደምጥ የቆየው ፍ/ቤቱም በእያንዳንዱ መዝገብ ትዕዛዝ የሰጠ ሲሆን በእነ አቶ መላኩ ፋንታ እና አቶ ገ/ዋህድ እንዲሁም የእነ ተመስገን ስዩም እና መልካሙ እንድሪያስን መዝገብ ክሱ በ13 ቀን ውስጥ እንዲቀርብ አዟል፡፡
የእነ መሐመድ ኢሣ እና ጥጋቡ ዓይዳ መዝገቦች ላይ ደግሞ ለነሐሴ 15/2005 ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡ ለነሐሴ 16 ከሰአት በኋላ ቀጥሯል፡፡ በተጨማሪም ወደ ማረሚያ ቤት እንዲወርዱ የተጠየቁት እንዲወርዱ እንዲሁም በማረፊያ ቤት እንዲያዩ ተጠየቁት በዚያው እንዲቆዩ ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል የከባድ ሙስና ወንጀል ተጠርጣሪ ባለሃብቶቹ ጠበቆች እና የፌደራሉ የስነምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን በኩባንያዎች አስተዳደር ጉዳይ ላይ ፍ/ቤቱ ባዘዘው መሠረት ተስማምተው፣ አስተዳዳሪ ባለማቅረባቸው ፍርድ ቤቱ ሐምሌ 30 ቀን 2005 በዋለው ችሎት በድጋሚ ተስማምተው እስኪቀርቡ ድረስ የኩባንያዎቹ አስተዳደር አሁን ባለበት እስከ መስከረም 22ቀን 2006 ዓ.ም ድረስ እንዲቀጥል ብይን ሰጠ፡፡
የተጠርጣሪ ባለሃብቶቹ ተወካዮችና ጠበቆች ለንብረቶቹ ገለልተኛ አስተዳዳሪ ሳይመደብ መቆየቱ ንብረቶች ያለ ባለቤት እንዲባክኑ ያደርጋል ብለው የተከራከሩ ሲሆን ፍርድ ቤቱ ሁለቱ ወገኖች ከመስከረም 22 ቀን 2006 በፊት ተስማምተው በማመልከቻ የሚያቀርቡ ከሆነ በፍ/ቤቱ አሠራር መሠረት የተሰጠው ብይን ተሽሮ የሚታይበት ሁኔታ እንደሚኖር አስገንዝቧል፡፡
የፍርድ ቤት ሂደት እልባት እስኪያገኝ ንብረታቸው በገለልተኛ አስተዳደር እንዲተዳደር ጥያቄ ቀርቦባቸው የነበሩት አምስት ኩባንያዎች፣ ንብረትነታቸው የአቶ ስማቸው ከበደ የሆኑት ኢንተርኮንቲኔታል ሆቴል እና ዲኤች ሰሜክስ ኃ.የተ.የግ.ማህበር፣ የአቶ ከተማ ከበደ ንብረት የሆነው ኬኬ ኃ.የተ.የግ.ማህበር፣ ንብረትነታቸው የአቶ ነጋ ገ/እግዚአብሔር የሆኑት ነፃ ኃላ.የተ.የግ.ማህበር እና ባሰፋ ትሬዲንግ ናቸው፡፡

. ኢህአዴግ - ትንግርታዊ እድገት አስመዝግቤያለሁ!
. ተቃዋሚ - አላየንም፤ እድገቱ የውሸት ነው!
. ህዝብ - መሃል ተቀምጦ ቁልጭ ቁልጭ!

ከጥቂት ዓመታት በፊት ነው፡፡ አንድ ዘመናዊ ካፌ ውስጥ ቁጭ ብዬ ያዘዝኩትን ማኪያቶ እየጠበቅሁ ነበር፡፡ (የምንጠብቀው ነገር አበዛዙ!) መጠበቁ ሲሰለቸኝ ከያዝኩት ቦርሳ ውስጥ ያጋመስኩትን አዲስ መፅሃፍ አውጥቼ ማንበብ ጀመርኩኝ፡፡ አንድ አምስት ገፆች ካነበብኩ በኋላ ነው ማኪያቶው የመጣልኝ (“የዘገየ ማኪያቶ እንዳልተጠጣ ይቆጠራል”) አስተናጋጁ የዘገየበትን ምክንያት ሊነግረኝ ወይም ይቅርታ ሊጠይቀኝ አልፈለገም፡፡ (ይቅርታ መጠየቅ የማይወዱት ፖለቲከኞች ብቻ ይመስሉኝ ነበር!) እሱ እቴ! ማኪያቶውን ወርውሮልኝ እብስ አለ፡፡
ደግነቱ ባሪስታው ባለሙያ ነው፡፡ ግሩም ማኪያቶ ነው የሰራልኝ፡፡

ተጨማሪ አምስት ገፆችን በማኪያቶዬ አወራረድኩና ሂሳብ ከፍዬ ለመሄድ፣ አስተናጋጁን በጭብጨባ ጠራሁት፡፡ ሂሳቡን ከተቀበለኝ በኋላ ጠረጴዛው ላይ ያስቀመጥኩትን ዳጐስ ያለ መፅሃፍ የጐሪጥ እያየ “ለቤቱ አዲስ ስለሆኑ ነው እንጂ ማንበብ ክልክል ነው” አለኝ፡፡ በትክክል የተሰማኝን ስሜት አላውቀውም፡፡ ንዴት… ግርምት… ግራ መጋባት… ሁሉም በአንድ ላይ የተደበላለቁበት ስሜት ሳይሆን አይቀርም፡፡ “አበዳችሁ እንዴ… እንዴት ማንበብ ትከለክላላችሁ?” አልኩት አስተናጋጁን፡፡
“እኔ የታዘዝኩትን ነው… ካላመኑኝ…” ብሎ ግድግዳ ላይ ወደተለጠፈ ማሳሰቢያ በእጁ ጠቆመኝ፡፡ ዓይኔ እጁን ተከትሎ ሄደ፡፡ “ጋዜጣ ማንበብ ክልክል ነው!” ይላል - ቃለ አጋኖው የደመቀው ማሳሰቢያ! ከአፌ አልወጣም እንጂ “ደንቆሮዎች!” ብያለሁ - በሆዴ፡፡ (ንዴት ነዋ!) “አንድ ሰሞን እኮ ቤቱ ላይብረሪ መስሎ ነበር… አንድ ማኪያቶ ይዞ መወዘፍ ነው!” አለኝ - የክልከላውን ምክንያት በግድምድሞሽ ሊያስረዳኝ የፈለገው አስተናጋጅ፡፡ “መቼ ይሆን ከክልከላ አባዜ” የምንላቀቀው? ለአፍታ ቆዘምኩ፡፡ ከመንግስት ጀምሮ እስከ እድር ቤት መጋዘን ኃላፊው መከልከል ብቻ ነው፡፡ በደንብ ሳስበው የሰነፍ መፍትሄ መስሎ ታየኝ፡፡ ፈጠራ ሲነጥፍ፣ አዕምሮ መስራት ሲያቆም የሚመረጥ ቀላል መፍትሄ፡፡ (ጦቢያን የሰነፎች አገር አድርገናታል!)
ይሄ የማንበብ ክልከላ ትዝ ያለኝ ለምን መሰላችሁ? አንድ ወዳጄ ሰሞኑን አንድ ምግብ ቤት ውስጥ ተለጥፎ ያነበበውን ማሳሰቢያ ነግሮኝ ነው፡፡ “ጉርሻ ክልክል ነው!” ይላል፡፡ (ጉድ ሳይሰማ… አሉ!) ይኸው “አትጐራረሱ!” የሚል ምግብ ቤት መጣና አረፈው! (“መሳሳም ክልክል ነው” የሚሉም አሉ፡፡) በእርግጥ እነዚህኞቹም ቸግሯቸው ነው፡፡ (ቢቸግር ጤፍ ብድር አሉ!) ምግብ ቤቱ ብፌ በማዘጋጀት ይታወቃል፡፡ አንዳንድ “ስማርት” ነን ባዮች ታዲያ ሁለት ሆነው ይገቡና የአንድ ሰው ምሳ አንስተው ይበላሉ - እየተጐራረሱ፡፡ ብፌ ላይ ደጋግሞ ማንሳት ስለሚፈቀድ፣ አንድ ምግብ ለሁለት ጥግብ እስኪሉ በልተው ይወጣሉ - የአንድ ብፌ ብቻ ከፍለው፡፡ ከምግብ ቤት ሃላፊዎቹ የተገኘ መረጃ ነው (from the horse’s mouth እንዲሉ) ሃላፊዎቹ ለዚህ ቢዝነስ የሚያቃውስ ችግር የመጣላቸው ፈጣን መፍትሄ ጉርሻን መከልከል ነው፡፡ የቢዝነስ ስትራቴጂ መሆኑ እኮ ነው! (ድንቄም ስትራቴጂ!)
አይገርማችሁም… ሁለቱም እኮ ጉርሻን “አቢዩዝ” እያደረጉ ነው - ተመጋቢውም መጋቢውም፡፡ አንዳንድ ብልጣ ብልጦች ጉርሻን ያለአግባብ ተጠቀሙበት ብሎ መጐራረስን መከልከል የሰነፎች መፍትሄ ነው፡፡ እንዴ… መጐራረስ እኮ “አንጡራ” ባህላዊ ሃብታችን ነው፡፡ (የውጭ ምንዛሪ ባያመጣም!) በነገራችሁ ላይ ፈረንጆች በጉርሻና በደቦ የአመጋገብ ባህላችን ይገረማሉ አሉ፡፡ (ጥሬ ስጋ መብላታችን እንደሚያስገርማቸው!) ጋዜጣ ማንበብ በይፋ የሚከለክል ካፌ እንዳለን ቢሰሙ ደግሞ የበለጠ ይገረሙ ነበር፡፡ (ኧረ “ዊርድ” ይሆንባቸዋል!) ምናልባትም የጥናትና ምርምር መነሻ ሊሆናቸውም ይችላል፡፡ (ሺ አመት ቢያጠኑን አያውቁንም!)
ይሄውላችሁ… አንድ ቀን አገር አማን ነው ብለን ካፌ ውስጥ ስንገባ ደግሞ “ሞባይል ማውራት ክልክል ነው!” የሚል ማሳሰቢያ እንዳናይና ተማረን ለስደት እንዳንነሳ (ስደቱም ካልተከለከለ እኮ ነው!) ሰሞኑን የጥላሁን ገሰሰ ልጅ በኢቴቪ “የማያውቁት አገር አይናፍቅም…” የሚለውን ዘፈን ሲያቀነቅን ሰምቼ አልዋጥልህ አለኝ፡፡ እንዴ… በዓመት ሩብ ሚሊዮን ገደማ ህዝብ አገሩን ጥሎ ወደማያውቀው አረብ አገራት እየሄደ እኮ ነው፡፡ የማያውቁት አገርማ በደንብ ይናፍቃል! ቢያንስ በጦቢያ
እኔ የምላችሁ…ሰሞኑን “አንድነት” ፓርቲ በሰላማዊ ሰልፍ ተንበሸበሸ አይደል? ምን ያድርግ? የስምንት ዓመት “ውዝፍ” አለበት እኮ! (የሰልፍ “ሃራራውን” እየተወጣ ነው!)
አንዳንድ ፖለቲካ - ቀመስ እንዲሁም ኢህአዴግ ዘመም ሰዎች፤ ተቃዋሚዎችን ሲተቹ “እነሱ ደሞ ያለተቃውሞ ሥራ የላቸውም” ይላሉ፡፡ እንዴ … ድሮም የተቋቋሙት ለ“መቃወም” አይደለም እንዴ? (ፈቃዳቸው እኮ የተቃውሞ ነው!) ያለዚያማ የኢህአዴግ “አጋር” ድርጅት መሆን ይችሉ ነበር፡፡ እናላችሁ… ጥያቄው መሆን ያለበት ለምን ተቃወሙ ሳይሆን “ምንድነው የተቃወሙት?” የሚለው ነው፡፡ (“ተቃውሞ ለተቃውሞ ሲባል” ወይስ? … የሚል ክርክር በኢቴቪ ቢጀመር ጥሩ ነበር!) ሌላው ደሞ “ለሚቃወሙት ነገር አማራጭ አላቸው ወይ?” የሚለው ጥያቄ ነው - ለተቃዋሚዎች የሚቀርብ፡፡ እንጂማ… መቃወም፣ መሰለፍ፣ መሰብሰብ፣ መቀስቀስ፣ መደራጀት፣ ማደራጀት፣ ማስፀደቅ ማሰረዝ… ሥራቸው እኮ ነው፡፡ (ህገመንግስቱ ያጐናፀፋቸው መብትም ጭምር!) ለምሳሌ የአንድነት ፓርቲው አቶ አስራት ጣሴ፤ በሰሞኑ የተቃውሞ ሰልፍ “እድገቱ የውሸት ነው!” ብለዋል (ሥራቸውም መብታቸውም ነው!) ኢህአዴግ ደግሞ እድገቱን በአሃዝና በዲጂት አስልቶ “የምር ነው” ይለናል፡፡ (እሱም መብቱ ነው!) እኛ ደሞ (ሰፊውን ህዝብ ማለቴ ነው!) መሃል ሆነን ቁልጭ ቁልጭ እንላለን (እኛም መብታችን ነው!)
“አንድነት” በሰሞኑ ሰልፍ ደረሰብኝ ያለውን ችግር ሰምታችኋል? ቅስቀሳ የሚያካሂድበት መኪና አራቱም ጐማዎች ባልታወቁ ግለሰቦች ተንፍሰው ተገኝተዋል፡፡ አንዳንዶች የኢህአዴግ ሴራ ነው ቢሉትም እኔ ግን ለመቀበል አቃተኝ (ኢህአዴግ መንግሥት እንጂ “አሸባሪ” ነው እንዴ?)
እኔ የምለው ግን… የፓርቲዎች “ሥነምግባር ኮድ” ምርጫ ከሌለ (election ማለቴ ነው!) አይሰራም እንዴ? (ሥነምግባር እኮ ለራስ ነው!) አንድነትም ግን መጠንቀቅ ነበረበት፡፡ ለምንድነው ለመኪናው ጠባቂ የማያቆመው? (ላቷን ውጭ እያሳደረች ጅብን ነገረኛ ታደርጋለች አሉ) በነገራችሁ ላይ ሰሞኑን ተቃዋሚዎች የሚያካሂዱት እንቅስቃሴ ለእነሱ ብቻ ሳይሆን ለኢህአዴግም ትልቅ ጠቀሜታ እንዳለው የልምድ ፖለቲከኞች (የልምድ አዋላጅ እንደሚባለው) ተናግረዋል፡፡ እኔም እስማማለሁ (እኔም እኮ የልምድ ፀሃፊ ነኝ) አያችሁ… እንቅስቃሴው ዲሞክራሲ እንዳለና የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት ግንባታ እየተጧጧፈ መሆኑን የሚያሳይ ነውና (የባቡር መስመር ዝርጋታውን ባያህልም!) ለመንግሥትም ሆነ ለኢህአዴግ የገፅ ግንባታ ያግዛቸዋል፡፡
ጀግናው አትሌት ኃይሌ ገ/ሥላሴ፤ ባለፈው እሁድ በኢቴቪ “120” መዝናኛ ፕሮግራም ስለ ፖለቲካ የተናገረውን ሰማችሁልኝ? እኔማ ምን አልኩ መሰላችሁ? “ኃይሌ አምርሯል!” እውነቴን እኮ ነው! የኃይሌ ወደ ፖለቲካ መግባት እርግጥ መሆኑን ያወቅሁት የዛን እለት ነው፡፡ (በኢቴቪ ደገመዋ!) ምን እንዳለ አልሰማችሁም? የፖለቲካ “እሳት አደጋ አጠፋለሁ” እኮ ነው ያለው፡፡
“ፖለቲካ እሳት አይመስለኝም፤ ከሆነም ገብቶ ማጥፋት ነው” ብሏል-አትሌቱ፡፡ (ችግሩ ውሃ እኮ ነው!) ውሃው ከተገኘ ግን እንደ ኃይሌ አይነት ብዙ የ“ፖለቲካ እሳት” አጥፊዎች ያስፈልጉናል፡፡ “የፖለቲካ አምቡላንስ” እና የ “የፖለቲካ ቀይ መስቀል”ም ቢገኝ … ሻርን ነበር፡፡ ጦቢያ ከ“ፖለቲካ እሳት አደጋ” ትድናለች ማለት እኮ ነው! (ቢያንስ ቃጠሎው ይቀንሳል!) ዜጐች በፖለቲካ እሳት ከመለብለብም ይድናሉ፡፡
ቀስ በቀስ ፖለቲካ እሳት ሳይሆን ውሃ ይሆናል - የበረደ፣ የሰከነ፣ የረጋ፡፡
የፖለቲካችን ባህርይው ብቻ ሳይሆን መልኩም ይለወጣል - ከ“ቀይ” ወደ “አረንጓዴ”፣ ከ“እሳት” ወደ “ውሃ”፣ ከብጥብጥ ወደ ሰላም፣ ከ “ሽብር” ወደ ልማት ይቀየራል፤ ያድጋል፤ ይሻሻላል፡፡ ለአረንጓዴው ፖለቲካ ያብቃን! (ከአትሌት ኃይሌ ጋር ወደፊት!)

(ሃርያ ላግድ ጐስያ ጐችድ ጌድዋ ካልዮጌ ዮሳመለቼስ)
ከዕለታት አንድ ቀን አያ አንበሳና ሰው ወዳጅ ሆኑ አሉ፡፡ “እዚህ ከምንቀመጥ ለምን በጫካ ውስጥ ዞር ዞር እያልን እግራችንን አናፍታታም” አለ ሰው፡፡
አንበሳም፤ “እኔ ጫካው ሰልችቶኛል፡፡ መንቀሳቀስ ከሆነ የፈለግከው ወደሚቀጥለው ከተማ እንሂድ”
ሰው፤ “መልካም፡፡ እየተዘዋወርን የከተማውን ሁኔታ እንይ”
በዚህ ተስማምተው መንገድ ጀመሩ፡፡
መንገድ ላይ ጨዋታ አንስተው ሲወያዩ የየራሳቸውን ዝርያ አንስተው ማውራት ጀመሩ፡፡
“እናንተ የሰው ልጆች’ኮ የእኛን የአንበሶችን ያህል ጥንካሬ የላችሁም፡፡ እኛ የዱር አራዊትን ሁሉ አስገብረን በእኛ ሥር እንዲሆኑ አድርገናል፡፡ እናንተ ግን እርስ በርሳችሁ እንኳን መስማማት አቅቷችሁ፤ ጦርነት፣ ዝርፊያና እልቂት ውስጥ ትገኛላችሁ” አለ አንበሳ፡፡
ሰውም፤ “አይደለም፡፡ እኛ የሰው ልጆች፤ የዓለምን ሥልጣኔ ለመምራት ሁልጊዜም ከላይ ታች ስንል፣ ያለውን ሃብት በጋራ ለመጠቀም፣ በእኩል ለመከፋፈል፣ ስንጣጣር ነው ግጭት የሚፈጠረው፡፡ ሌላው ቀርቶ አንተ የምትኖርበትን ጫካና ደን እንዳይጨፈጨፍ ባንታገል ኖሮ ይሄኔ መኖሪያ አጥተህ ነበር” ይለዋል፡፡
አንበሳም፤
“እሱ ለእኛ በማዘን ሳይሆን የራሳችሁን ህይወት ለማራዘም ስትሉ የምታደርጉት ነው፡፡ እኛ የተፈጥሮ ጥንካሬያችን ብቻ ያኖረናል”
ሰው፤ “በሽቦ በታጠረ መናፈሻ ውስጥ እንድትኖሩ የእንስሳት ማቆያም እኮ አዘጋጅተንላችኋል፡፡ አንበሳ፤ “እሱም ቢሆን እኛን ለቱሪስት እያሳያችሁ ገንዘብ የምትሰበስቡበት ነው፡፡ ለእኛ እሥር ቤት ነው”
በዚህ ማህል አንድ አደባባይ ጋ ይደርሳሉ፡፡ አደባባዩ መካከል ሐውልት አለ፡፡ ሐውልቱ አንድ ሰው አንድ አንበሳን ታግሎ ሲጥለው የሚታይበት ስዕል አለው፡፡
ይሄኔ ሰውዬው በአሸናፊነት ስሜት፤
“ተመልከት፤ የሰው ልጅ አንበሳን እንዴት እንደሚያሸንፈው!” አለው፡፡
አንበሳም፤ “ይሄ ያንተ አመለካከት ነው፡፡ ይህንን ሐውልት የሠራነው እኛ አንበሶች ብንሆን ኖሮ፣ አንበሳውን ከላይ፣ የሰውን ልጅ ከታች አድርገን እንቀርፀው ነበር!” አለው፡፡
***
ሁሉ ነገር ሁለት ወገን እንዳለው አንርሳ፡፡ ከማን አቅጣጫ ነው የምንመለከተው ነው፤ ጉዳዩ፡፡ ሁሉም እኔ ነኝ ጠንካራ ይበል እንጂ ጠንካራው በመካያው ይለያል፡፡ ዕውነተኛው፤ የማታ የማታ መለየቱ የታሪክ ሂደት ነው፡፡
“ዳገት ከላይ የሚያዩት ቁልቁለት፣ ቁልቁለት ከታች የሚያዩት ዳገት” እንዳለው ነው ገጣሚው፡፡
መቼ ቁልቁለቱ ዳገት እንደሚሆንብን ካላስተዋልን “ያሰፈሰፈው መዓት” ይጠብቀናል (The impending catastrophe እንዲሉ)፤
ሐውልቱን፤ ጊዜ የሰጠው ይሠራዋል፡፡ አንድ የቀድሞ የደርግ ጄኔራል በሰጡት ኢንተርቪው፤ “ስለደርግ በሚያወራ የቴሌቪዥን ፕሮግራም በቀዳሚነት የሚታዩት እርሶ ነዎት - ውስኪ ሲጠጡ፡፡ ምን ይሰማዎታል?” ቢባሉ፤ “ይሄ ምንም አይገርምም፡፡ እኛ በጊዜያችን ውስኪ ጠጣን! እነሱም ይሄው በጊዜያቸው ውስኪ እየጠጡ ነው” ብለው መልሰዋል፡፡ ጊዜ ፈራጅ ዳኛ ነው፡፡
ዛሬም የሀገራችን ቁልፍ ጉዳይ መቻቻል ነው፡፡ መቻቻል ብስለትንና ዕውቀትን አጣምሮ የያዘና ጊዜን በቅጡ ግንዛቤ ውስጥ የሚያስገባ ዕሳቤ ነው፡፡ መልካም ባሕል ያለው ህዝብ የታደለ ነው፡፡ የባህሉ ጥንካሬ ለመቻቻሉ ብርቱ አስተዋጽኦ ያደርጋል፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ እንደዚያ ነው፡፡ እኔ ብቻ ነኝ ጠንካራ የሚል አመለካከት ከመቻቻል ጋር ግንባር ለግንባር ይጋጫል፡፡ “እኔ ነኝ የበላይ” የሚል አስተሳሰብን ያመላክታልና፡፡ መካረርና ማክረር ከጽንፈኛና ከፅንፈኝነት ጐራ መክተቱ እውን ነው፡፡ መጭው ነገር አስቀድሞ ጥላውን ይጥላል፡፡ (Coming events cast their shadows) እንደሚሉት ፈረንጆች) (ለላመት የሚቆስል እግር ዘንድሮ ዝምብ ይወረዋል፤ እንዳለውም አበሻ)
የሩቁን ያላስተዋለ አለቃ፣ ኃላፊ ወይም መሪ፣ አስተውሎም ያላመዛዘነ፤ አመዛዝኖም በጊዜ እርምጃ ያልወሰደ ከሆነ፤ በአደጋው ውስብስብ መረብ ውስጥ ገብቶ መተብተቡ አይቀሬ ነው፡፡ ብርቱ ጥንቃቄ ያሻል፡፡ ስለዲሞክራሲ መጠንቀቅ ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ስለሃይማኖት መጠንቀቅ የበለጠ ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ሰው እንደቤቱ እንጂ እንደጐረቤት አይኖርምና ሁሉም ወገን ሊያስብበት የሚገባ ጥልቅና ጥብቅ ጉዳይ ነው፡፡
እንደተጣደ ወተት መቼ ሊገነፍሉ እንደሚችሉ የማናውቃቸውን ነገሮች በዐይነ-ቁራኛ ማየት፤ ተገቢውን ማርከሻ ማወቅና መጠቀም ተገቢ ነው፡፡ እንደ ሙስና፣ ኢፍትሐዊነት፣ የዕምነት - ሽፋን ሂደቶች… ወዘተ ጉዳዮች በትኩረት መጤን ያለባቸው ናቸው፡፡
ሬዲዮው ያወራል በተግባር ምንም የለም፡፡ ቴሌቪዥኑ ያሳያል በተግባር የለም፡፡ ጋዜጣ ይፅፋል በግብር ምንም የለም፡፡
The rottener the time the easier it is to get promoted ይላል ሔልሙት ክሪስት የተባለ ፀሐፊ፡፡ (ጊዜው ወይም ዘመኑ እየተበሳበሰ ሲሄድ የሥራ ዕድገትና ሹመት በሽበሽ ይሆናል እንደማለት ነው፡፡) የተሾምንበት፣ የአደግንበት ሥራ ተግባርን ግድ እንደሚል ደጋግመን እናስብ፡፡ ምን አልሠራንም የምንለውን ያህል የሠራነው ተገቢ ነወይ? ብለንም ለመጠየቅ እንትጋ!
የትውልድ ዝቅጠትና መበስበስ (decadence) የፖለቲካውና የሶሺዮ ኢኮኖሚው ድቀት የሚያመጡት ክስተት ነው፡፡ እጅግ በከፋ ገፁ ሲታይ ከሀገራችን ከውይይት ይልቅ ግጭት፣ ከሰላም ይልቅ ጦርነት ይዘወተራል፡፡ በእንዲህ ያለው ዘመን አፍ ይበዛል፡፡ አዕምሮ ይደርቃል፡፡ አንድ ደራሲ እንደሚለው verbal diahria and mental constipation በይፋ ይታያል፡፡ (የአፍ - ተቅማጥና የአዕምሮ - ድርቀት ይንሰራፋል እንደማለት ነው፡፡ መለፍለፋ፣ መለፍለፋ፣ መለፍለፋ ብቻ፡፡ ሐሳብ የለም፡፡ ዕውቀት የለም፡፡ ጥበብ (wisdom) የለም፡፡ ተግባር - አልባ ልፍለፋ! ለዚህ ነው ከልኩ በላይ የተመኘነው ለውጥ በቀላሉ የማይመጣው፡፡ የአፍ መብዛት፣ የስብሰባ መብዛት… የግምገማ መብዛት ብቻውን ፍሬ እንደማያፈራ ደጋግመን ተናግረናል፡፡ የሚሰማ አለመኖሩ ነው ምላሹ፡፡
“የምንለውን ብለናል የምናደርገውን እንጀምር!” አሉ አሉ የቀድሞው መሪ፡፡ ስላልን የሠራን እንዳይመስለን ነው ነገሩ፡፡
“አህያ እየነዱ፣ ቅል እየሳቡ፣ ከኋላ ሲከተሉ፤ ወተት ያለቡ ይመስላል” የሚለው የወላይታ ተረት ሁኔታውን የበለጠ ይገልፀዋል፡፡

Published in ርዕሰ አንቀፅ

ፍቅረኛ በምትልከው ገንዘብ ሌላ ትዳር መመስረት ተለምዷል
ፍቅረኞቻቸው በሚፈፅሙባቸው ክህደት ለሞትና ለእብደት የተዳረጉ ሴቶች አሉ

ትዕግስት ገብሬ የሰላሳ አመት ወጣት ሳለች ነበር ወደ ቤሩት ያቀናችው- በ1997 ዓ.ም፡፡ ግድ ሆኖባት ነው እንጂ ለአምስት ዓመት አብራው የዘለቀችውን የትምህርት ቤት ፍቅረኛዋን ሚካኤል ሃይሉን ትታ መሄድ አልፈለገችም ነበር፡፡ “በምድር ላይ እንደሱ የማፈቅረውና የማምነው ሰው አልነበረም” ትላለች፡፡ ለነገሩ ወደ ቤሩት የሄደችውም ትንሽ ሰርታ ጥሪት በመቋጠር ከሚካኤል ጋር ትዳር ለመመስረት ነበር፡፡ በቤሩት በቆየችባቸው ሁለት ዓመታት ቢያንስ በሳምንት ሁለት ጊዜ፣ ሚካኤል ጋር በመደወል ናፍቆቷን ትወጣለች፤ ወደፊት ስለሚመሰርቱት ትዳርም በሰፊው ያወራሉ፡፡
ትዕግስት በቤት ሰራተኝነት ተቀጥራ እየሰራች የምታገኘውን ደሞዝ፣ አብዛኛውን ለሚካኤል እየላከች፣ ጥቂቱን ለቤተሰብዋ ትልክ ነበር፡፡ የሁለት አመት የስራ ኮንትራትዋ ሲያልቅ ፍቅረኛዋ ጋ ደውላ “ልመጣ ነው” አለችው፡፡ ሚካኤል ደነገጠ፡፡ በዚህ ፍጥነት ትመጣለች ብሎ አላሰበም፡፡ እናም ማግባባት ያዘ - እዚያው እንድትቆይለት፡፡ “አንዴ በደንብ ስሪ እና ደህና ገንዘብ አጠራቅመን እንጋባለን” አላት፡፡ የሱ ነገር ሆነባትና ሃሳቡን ተቀብላ ፣ ኮንትራትዋን ለሁለት ዓመት አደሰች፡፡ ከዚህ ጊዜ በኋላ ግን የፍቅረኛዋ ባህርይ እየተለወጠባት መምጣቱን ትዕግስት ታስታውሳለች፡፡ እንደ በፊቱ ስትደውል አታገኘውም፡፡

አንዳንዴ ስልኩ ዝግ ይሆናል፡፡ አንዳንዴ ደግሞ አይነሳም፡፡ ያነሳላት ጊዜ “ምን ሆነህ ነው?” ስትል መጠየቋ አልቀረም፡፡ ሰበብ አያጣም፡፡ ወይ “ተኝቼ ነበር” አለያም “አልሰማሁትም” ይላታል፡፡
ትዕግስት ጆሮ አልሰጠቻቸውም እንጂ ቤተሰቧ ፍቅረኛዋን በተመለከተ አንዳንድ ጥርጣሬያቸውን ነግረዋታል፡፡ ግን እንዴት ብላ የአምስት ዓመት የፍቅር አጋሯን ትጠርጥረው! ትዕግስት በአጠቃላይ ለአራት አመት ያህል ከሰራች በኋላ “አሁንስ በቃኝ” ብላ ወደ አገሯ ለመምጣት ቆረጠች፡፡ ፍቅረኛዋ ግን አሁንም መመለሷን አልፈለገውም፡፡ እዚያው ትንሽ እንድትቆይ ሃሳብ አቀረበ፡፡ እሷ ግን አገሯ መጥታ ከምትወደው ፍቅረኛዋ ጋር በትዳር ለመተሳሰር ቸኩላለች፡፡ እናም ዝም ብላ ወደ ሀገሯ ተመለሰች፡፡ትዕግስት አገሯ እንደመጣች ፍቅረኛዋን አላገኘችውም፡፡ “ለንግስ ወደ አንድ ገዳም ሄጃለሁ” የሚል መልዕክት ትቶላት ነበር፡፡ የናፈቃትን የወደፊት ባሏን ያገኘችው ከሳምንት በኋላ ነበር፡፡ በተገናኙ ሰዓትም ተቃቅፈው መላቀሳቸውን ታስታውሳለች - በናፍቆት፡፡
ሚካኤል ትእግስትን ካገኛት ቀን ጀምሮ “ኢንተርኔት ቤት ከፍተን እንስራ” እያለ ይወተውታት እንደነበር ትናገራለች፡፡ ይሄኔ ነው ስትልክ የነበረውን ገንዘብ የት እንዳደረገው የጠየቀችው፡፡ “ላስደስትሽ ብዬ ቤት መስራት ጀምሬአለሁ” ሲል መለሰላት፡፡ በደስታ ጮቤ ረገጠች፡፡ ወዲያው የጠየቃትን ኢንተርኔት ቤት ለመክፈት አስር ሺህ ብር ሰጠችው - ቤት እንዲከራይ፡፡ ገንዘቡን እጁ እንዳስገባ ተጣድፎ መውጣቱን የምትናገረው ትዕግስት፤ ከጥድፊያው የተነሳ ሞባይሉን እንኳን ይዞ አልሄደም ትላለች፡፡

ይሄ ሞባይልም ነው ጉዱን ያወጣበት ፡፡ ትዕግስት ሞባይሉ ስክሪን ላይ አንድ ፎቶ አየች፡፡ ህፃን ልጅ ያቀፈች ሴት ናት፡፡ ታውቃታለች፡፡ የገዛ ጓደኛዋ ቤቴል፡፡ እንዴት ፍቅረኛዋ ሞባይል ላይ የጓደኛዋ ፎቶ እንደተገኘ የሚነግራት ሰው ግን አላገኘችም፡፡ ቤሩት እያለች ስለ ቤቴል ስትጠይቀው “አንገናኝም፤ አግብታ ሌላ ቦታ ነው የምትኖረው” የሚል ምላሽ እንደሰጣት ታስታውሳለች፡፡ ቤቴልም ራሷ የትዕግስትን ስልክ ማንሳት ካቆመች ሶስት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ በጥያቄና ግራ በመጋባት ብዙ ዋለለች፡፡ በዚህ መሃል የሚካኤል ስልክ ጠራ፡፡ “my love” ይላል - ጥሪው፡፡ በደመነፍስ ስልኩን አነሳችው፡፡
“ሄሎ”
“ሄሎ ማን ልበል?” ደዋይዋ ናት
“ሞባይሉን ቻርጅ እያደረገው ነበር… ማን ልበል?” ትዕግስት የቤቴል ድምፅ መሆኑ አልጠፋትም፡፡
“ባለቤቱ ነኝ፤ ገዳም በሰላም መድረሱን ለማወቅ ነው” የደዋይዋ ምላሽ ነበር፡፡
“እኔም ባለቤቱ ነኝ አንቺ ማነሽ?” አለች ትዕግስት ለቅሶ በተቀላቀለበት ድምፅ፡፡
ከዛ በኋላ ያደረገችውን አታውቀውም፡፡ ግን ታማ ለአስር ቀን ፀበል ተመላልሳለች፡፡ ለካ ፍቅረኛዋ ከገዛ ጓደኛዋ ወልዷል፡፡ ትዕግስት በምትልከው ገንዘብም ትዳር መስርቶ አዲስ ህይወት ጀምሯል፡፡ ቤት እየሰራሁ ነው ያላትም ውሸቱን እንደሆነ ገባት፡፡ ትዕግስት ከሁለት ያጣ ሆነች፡፡ ገንዘቧንም ፍቅሯንም ተነጠቀች፡፡ ጊዜዋ በከንቱ መባከኑ አበገናት፡፡ ከዚህ በኋላ እንደ አዲስ ፍቅረኛ ይዛ፣ ወደ ትዳር ለመግባት የእድሜዋ ጉዳይ አሳስቧታል፡፡ መውለድ ባልችልስ? እድሜዬ ቢያልፍስ? … ትብሰለሰላለች - በቁጭት፡፡
ሚካኤል ያንን ሁሉ በደል ፈፅሞባት አሁንም መደወሉን አላቆመም፡፡ “ከፈለግሽ ከእኔ መውለድ ትችያለሽ፤ ቤሩት ሄደሽ ሰርተሽ ነይ እንጂ እሷን ፈትቼ አገባሻለሁ” እያለ ይጨቀጭቀኛል ትላለች - በሃዘን ተውጣ፡፡
ደብረዘይት ተወልዳ ያደገችው ሰናይት ሃይሉ፤ ከፍቅረኛዋ ከወርቁ ጋር በ1999 ዓ.ም መጨረሻ ላይ እንደተጋቡ ትናገራለች፡፡ በቂ መተዳደርያ ገቢ ግን አልነበራቸውም፡፡ ለዚህም ነው ባለቤቷ፣ ቤሩት ሄዳ በመስራት ትንሽ ገንዘብ ይዛ እንድትመጣ ሃሳብ ያቀረበው፡፡ ቤተሰቦቿ ሃሳቡን ባይደግፉትም ሠናይት ግን በባሏ ምክር ተሸንፋ ወደ ቤሩት ተጓዘች፡፡
ቤሩት ከገባች ጀምሮ በየሳምንቱ እየደወለች ባለቤቷን ታገኘው ነበር፡፡ ሙሉ ደሞዟን የምትልከውም ለእሱ ነበር፡፡ አንድ ዓመት ከሶስት ወር ከሰራች በኋላ ግን ያልታሰበ ነገር ተፈጠረ፡፡ አሰሪዎቿ ለእረፍት ወደ ሌላ አገር ሲሄዱ አብራ መሄድ አልፈለገችም፡፡ ስለዚህ እሷም ድምጿን አጥፍታ ለእረፍት ወደ ኢትዮጵያ መጣች፡፡ ቤቷ ግን ኦና ነበር፡፡

ወርቁ የለም፡፡ ቤተሰቧን ጠየቀች፡፡ የሄደበትን አውቃለሁ የሚል ጠፋ፡፡ እሷ ግን ፍለጋዋን አላቆመችም፡፡ የማታ ማታ ወርቁ በጓደኞቹ በኩል ደብዳቤ ላከላት፡፡“አትረብሺኝ፤ እኔ አግብቻለሁ፤ የራስሽን ኑሮ መምራት ትችያለሽ፤” ይላል የደብዳቤው መልዕክት፡፡ ሠናይት የምትሆነውን አጣች፡፡ ድንጋጤ፣ ዱብዕዳ፣ ሀዘን፣ ፀፀት፣ እልህ… በየተራ ተፈራረቁባት፡፡ በመጨረሻ ወርቁ የሚኖርበትን አካባቢ አጠያይቃ በመሄድ በጩቤ እጁ ላይ ወጋችው፡፡ ጉዳቱ ብዙ ባይሆንም መደንገጡና መፍራቱ አልቀረም፡፡ የመኖሪያ አካባቢውን ቀየረ፡፡ የዕረፍት ጊዜዋ ቢያልቅም ወደ ቤሩት መመለስ አልፈለገችም፡፡ ከሁሉም በላይ ሰው ቤት ሰርታ ያመጣችውን ገንዘቧን መብላቱ እንደሚያንገበግባት ትናገራለች፡፡ በቤተሰብና በጓደኞቿ ምክርና ግፊት ወደ ቤሩት ተመልሳ የሄደችው ከአንድ አመት በኋላ ነበር፡፡

አሁን ከቤሩት መጥታ የስጦታ እቃዎች መሸጫ ሱቅ ከፍታ እየሰራች ነው፡፡ ሰናይት፤ ቤሩት የምታውቃት አበራሽ የተባለች ወጣት የገጠማትን ተመሳሳይ አሳዛኝ ታሪክ አውግታናለች፡፡ አበራሽ እዚህ ሳለች ከፍቅረኛዋና ከአንድ ልጃቸው ጋር ነበር የሚኖሩት፡፡ ዘውዲቱ የተባለችውን የአገርዋን ልጅም አስጠግታት አብራት ትኖር ነበር፡፡ ለሰናይት እንደነገረቻት፤ ወደቤሩት ስትሄድ የልጅዋን ነገር አደራ የሰጠችው ለዚህችው አብሮ አደጓ ነበር፡፡
አበራሽ ስለ ፍቅረኛዋ አውርታ አትጠግብም የምትለው ሰናይት፤ እየሰራች ደሞዟን ለፍቅረኛዋ ትልክ እንደነበር ታውቃለች፡፡ ቤሩት በመጣች በስምንተኛ ወሯ ግን ዘውዲቱ ከፍቅረኛዋ ማርገዟን ሰማች፡፡ ፍቅረኛዋ የጋራ ልጃቸውን ለእናቷ ሰጥቶ ከአገርዋ ልጅ ጋር ትዳር መስርቷል፡፡ አበራች የሰማችውን መርዶ መቋቋም አልቻለችም፡፡ ህሊናዋን ሳተች፤ ጨርቋን ጥላ አበደች፡፡ በቤሩት ጐዳናዎች ራቁቷን መታየት ጀመረች፡፡ ሀገሯ እንድትመለስ ኤምባሲውን ማነጋገራቸውን የጠቀሰችው ሰናይት፤ ከኤምባሲው መፍትሄ አለመገኘቱንና ኋላም ሆስፒታል ገብታለች መባሉን እንደሰማች፣ ከዛ በኋላ ግን ያለችበትን እንደማታውቅ ትናገራለች፡፡
የሳዕዳ ታላቅ እህት ሃቢባ ጀማል፤ ወደ ሳውዲ አረቢያ የሄደችው ባለፈው አመት ነበር፡፡ ከመሄዷ በፊት ግን እቤታቸው ተከራይቶ ከሚኖረው ፍቅረኛው ጋር ኒካ (ቀለበት) ማሰሯን እህቷ ሰዓዳ ትናገራለች፡፡ ፍቅረኛዋን እንደነፍሷ ትወደው ነበር የምትለው ታናሽ እህቷ፤ አንድ አመት ሙሉ የሰራችበትን ገንዘብ ለእሱ እንደላከችለት ትገልፃለች፡፡
የሃቢባ ፍቅረኛ እነሱ ጋ ቤት ተከራይቶ ቢኖርም ከቤተሰቡ ጋር ብዙም እንደማይቀራረብ የምትናገረው ሳዕዳ፤ ከክፍለአገር የመጣች የአክስታቸው ልጅ ከእሱ ጋር በጣም ተቀራርበው እንደነበርና ይህንንም ቤተሰቡ ለሃቢባ መግለፁን ታወሳለች፡፡ በሰማችው የደነገጠችው ሃቢባ፤ ወዲያው ፍቅረኛዋ ጋ ትደውልና “እሷን ልጅ ብዙ አትቅረባት፤ ክፍለሃገርም ስሟ ጥሩ አይደለም” በማለት ቤተሰቡ ከጠረጠራት ዘመዷ ልታርቀው ሞከረች፡፡ ግን አልተሳካላትም፡፡ “ከዚህ በኋላ የሚያገባሽ ነገር የለም፤ አንቺን እንደውም አልፈልግሽም፤ ማግባት የምፈልገው እሷን ነው” ሲላት ከምትሰራበት ቤት አራተኛ ፎቅ ላይ ስልኩን ጆሮዋ ላይ እንደያዘች ወድቃ፣ ህይወቷ ማለፉን እህቷ በእንባ እየታጠበች ነግራናለች፡፡
እንዲህ ዓይነት አሳዛኝ የሴት እህቶቻችን ታሪኮች ጥቂት አይደሉም፡፡ የሚያሳዝነው ወደ አረብ አገራት የሚጓዙ ሴቶች እዚያ በሚያዩት በደልና ስቃይ ሳያንሳቸው እዚህም ሌላ ፈተና መጋፈጣቸው ነው፡፡ የሴት እህቶቻችን መከራ የሚቆምበት ጊዜ ይናፍቃል፡፡

በፖሊስና ተቃውሞ ባሰሙ ወጣቶች በተፈጠረው ግጭት በርካቶች ቆስለዋል
በበርበሬ ተራ አካባቢ የነበረው ግጭት ከፍተኛ ነበር

በአወሊያ ት/ቤት በእስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ዙሪያ፣ ከዚያም አልፎ በአክራሪነትና በሃይማኖት ነፃነት ጉዳይ፣ ሲብስም የፖለቲካ ጥያቄዎች እየተጨመሩበት ሲብላላ የቆየው አለመግባባት ወደ ግጭት የተሸጋገረው ከአመት በፊት የረመዳን የፆም ወቅት ቢሆንም፤ ባለፈው ሃሙስ እለት የኢድ በዓል ላይ የተፈጠረው ግጭት ብዙ ሰዎችን ለጉዳት የዳረገና ከሁለት ሺ በላይ ሰዎች የታሰሩበት ሆኗል፡፡ 
ሃሙስ ጠዋት በአዲስ አበባ ስታዲየም እና በዙሪያው ባሉ ጎዳናዎች የተከበረው የኢድ በዓል ላይ የተቃውሞ እንቅስቃሴ እንደሚካሄድ ቀድሞም ሲጠበቅ የነበረ ነው፡፡ የተቃውሞ እንቅስቃሴው አስተባባሪዎች በበራሪ ወረቀትና በኢንተርኔት የተቃውሞ ጥሪ ሲያስተላልፉ ሰንብተዋል፡፡ በስታዲየምና በዙሪያው የኢድ በዓል ስነ ስርዓት እንደተጠናቀቀ፣ የተቃውሞ አስተባባሪዎች ድምፅ የተሰማው ስታዲየሙ ውስጥ ሲሆን፣ በየአካባቢውና በዙሪያው ባሉ ጎዳናዎች ተስፋፍቶ ተስተጋብቷል፡፡

አጀማመሩ ላይ ግጭት አልተፈጠረም፡፡ የተቃውሞ ድምፅ እያሰሙ የሚጓዙትና በየአቅጣጫው የተሰማሩ ፖሊሶች ሲገጣጠሙ ነው ግጭት የተፈጠረው፡፡ በተለይ ከስታዲየም ወደ ሲኒማ ራስና አውቶቡስ ተራ፣ ወደ ፒያሳና መርካቶ፣ ወደ ባምቢስና ፍላሚንጎ በሚወስዱ አቅጣጫዎች ከተፈጠሩት ግጭቶች ሁሉ ወደ መርካቶና አውቶቡስ ተራ በሚወስደው በርበሬ ተራ አካባቢ የነበረው ለበርካታ ሰዓታት የዘለቀና የከፋ ነው፡፡
በየቅያሱና በየሰፈሩ ጭምር ዱላ በያዙ ፖሊሶችና ድንጋይ በሚወረውሩ አካባቢው ተረብሾ የዋለ ሲሆንና በየጎዳናው ላይ የሚታየው ትዕይንት የግጭቱን ስፋት ያሳያል፡፡
የተወረወሩ ድንጋዮች መንገዱን ሸፍነውታል፡፡ በፖሊስ የተደበደቡ ወይም በድንጋይ የተፈነካከቱም ሞልተዋል፡፡
በረብሻው ወቅት ከየአቅጣጫው በፖሊስ እየተያዙ የሚመጡ ሰዎች ትንሿ ስታዲየም ውስጥና ፖስታ ቤት አካባቢ ባለው ፓርክ ውስጥ ነበር ታስረው እንዲቆዩ የተደረገው፡፡ ችግር ፈጥረዋል ተብለው በሁለት ቦታዎች ተይዘው የነበሩ ሰዎች ቁጥር 3ሺ ይደርሳሉ ተብሎ የሚገመት ሲሆን ከፊሎቹ አመሻሽ ላይ ተለቀዋል፡፡ ቀሪዎቹ ግን በየክፍለ ከተማው በእስር እንዲያድሩ ተደርጓል፡፡ ባለፉት ሳምንታት መጀመሪያ በአንዋር መስጊድ ከዚያም በቦኒ መስጊድ እና በቶፊክ መስጊድ ሦስት ተቃውሞዎች መካሄዳቸው ይታወሳል፡፡
“የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች ይፈቱ”፣ “የደሴው ሼህ ግድያ ድራማ ነው”፣ “መጅሊሱ (ምክር ቤቱ) እኛን አይወክልም”፣ “ምርጫው ፍትሀዊ አይደለም”፣ “በ22 ዓመታት ውስጥ ኢትዮጵያን ያስተዳደረ ሙስሊም የለም”፣ “አህበሽ የተባለው አስተሳሰብ ይቅር”፣ “መንግስት በሀይማኖት ጣልቃ አይግባ”፣ “አወሊያ የሙስሊሙ ተቋም ነው” የሚሉ ጥያቄዎችና መፈክሮች ሲስተጋቡም ቆይቷል፡፡

Published in ዜና
Saturday, 10 August 2013 10:33

ለካ ሞት ግጥም አይችልም!!

እንደመግቢያ
ክፍት የሥራ ቦታ
ግጥም ፅፌ ፅፌ፣
አላነብም ብሎ ሰዉ ቢያስቸግረኝ
“ክፍት የሥራ ቦታ”፣ የሚል ከባድ ርዕስ-ያለው ግጥም ፃፍኩኝ!
ማ ጮክ በል አለኝ?... ተሻማ ህዝብ ሁሉ፣ግጥሜን ገዛልኝ!
በየቤቱ ሄዶ-ተስገብግቦ ጠግቦ፣ ዋለበት ቢመቸው-
ሦስቴ አራቴ፣ አምስቴ፤ ደጋግሞ አነበበው-
ግጥሙ እንዲህ አለቀ፡-
“ውድ አንባቢዬ ሆይ በቢሮ፣ በቤትህ፣ በፍራሽ ላይ ያለህ
መንግስት ያላየውን፣ ውለታ ዋልኩልህ፡፡
ምሁር ያልተካነው፣ ትምህርት አስተማርኩህ፡፡
ትግል ያልፈታውን፣ ቅን መላ ሰጠሁህ፡፡
ይህን በማንበብህ፣ የሥራ-አጥ ቁጥር፣ በጦቢያ ቀነሰ
ቢያንስ የዛሬውን ቀን፣ ስራ በማግኘትህ የልብህ ደረሰ!!
ግጥሜም ስራ አገኘ የአንጀት አደረሰ
እኔም ስራ አገኘሁ ምኞቴ ታደሰ!!
የዕድሜ ሙሉ መክሊት፣ ለዛ ነው አስቤዛ
እንዲህ ያለው ስራ በዋዛ አይገዛ!!

ውለሃል በል አንጋ
ፌዝ አይደለም ቅኔው፣የስራ ፍለጋ
ስራ ስትፈልግ ብቅ በል እኔጋ!...
ልምድ ይኑር አይኑርህ
አበባም ሁን ቀጋ
ወለላም ሁን ፉንጋ
ደማም ሁን ጠሟጋ፤
ወጣት ሆይ ነብር ጣት! ልክ እንደተመረቅክ፣ ብቅ በል ግጥም ጋ!!
ማስታወቂያ መስሎት ይህን ግጥሜን ሰምቶ
“ስራ እፈልጋለሁ” ብሎ ተሟሙቶ
ሞት መምጣቱን ሰማሁ እሱም ስራ ሽቶ!....
(ለዓለም ባንክ እና ለስራ - አጡ ወጣት እንዲሁም ለፀጋዬ ገ/መድህን
ሐምሌ 2005ዓ.ም
ለካ ሞት ግጥም አይችልም
ሰሞኑን፣
ሞትን መንገድ ላይ አየሁት፡፡
አለባበሱ ገረመኝ፡፡
ዥጉርጉር ቲ-ሸርት አድርጓል
ከታች ራንግለር ለብሷል!
አሃ?!
እሱም ፋሽን ይከተላል? ፍንዳታ መሆን ያምረዋል?
ያው እቲ-ሸርቱም ላይኮ፣ ከፊቱም ገፅ፣ ከኋላውም፤
መፈክር መሳይ ተፅፏል፡፡
ከፊት ለፊቱ በኩል፣ long live death ይላል
“ሞት ለዘላለም ይኑር”
ከጀርባው follow me ይላል “ተከተይኝ” ስለፍቅር!
ወይ ጉድ፤ ይሄስ ሞት ይገርማል!
ይሄ ጅል የጅል ቆንሲል
እሱም ህይወት ይፈልጋል?
ፍቅረኛ ማግኘት ያምረዋል?
ሞት፤የብርሃን ባላንጣ፣ ፀሀይ ይፈራል መሰል
ጥቁር ዣንጥላ ዘርግቷል፡፡
በእጁ ደሞ እንደወጉ፣ ደብተርና እርሳስ ይዟል!
እኔ፤ ገጣሚው ልቅሶ ቤት፤ ልቤን ላነባ ስገባ
ሞትም ተከትሎኝ ገባ፡፡
እኔ ወዲህ ማዶ ቆምኩኝ
እሱ ወዲያ ማዶ ቆመ
ከማህል ገጣሚው አለ
የፊደል አርበኛ አደለ? አስከሬኑ ጃኖ ለብሷል
ገጣሚ ማለት ፈሣሽ፣ ስደተኛ ወንዝ አደለ?-
ወንዝ አለት እንደሚንተራስ፣ ብረት ሳጥን ተንተርሷል፡፡
ሞትን ከገጣሚው ማዶ፣ በስሱ አሻግሬ እያየሁ፣
“ለምን መጣህ?” ብዬ ብለው
ሞት ፈጣጤ አፍ-አውጥቶ
“ግጥም ልማር!” አለኝ ኮርቶ፡፡
ይሄኔ ገጣሚው ነቃ!
አስክሬኑ ተግ አለና
ብድግ አለ ከተኛበት!
ሞትን በደም ዐይኑ አየና
“ሀጠራው!” አለ
‘ሞት ለዘላለም ይኑር!’
የሚል ሸቃባ መፈክር
እርኩስ ደረትህ ላይ ፅፈህ
ግጥም መማር ታስባለህ?
ግጥም የህያው ልሣን ነው፣ ለሞት አንደበት አይሆንም፡፡
የስንኝ ጠበል እሚፈልቅ፣ በድን አለት ውስጥ አደለም፡፡
ግጥም ከነብስ ቃል እንጂ፣ ከሥጋ ትንፋሽ አይነጥብም፡፡
አንዳች ህይወት ውስጥህ ሳይኖር፣ ፊደል በመቁጠር አትገጥምም!!
አንተ ግንዝ ነህ ግዑዝ!
ጥላ የነብስ ባላንጣ
ዛሬ ደግሞ ብለህ ብለህ፣ ግጥም ልትማር ትመጣ?
ሀጠራው! ዐይን - አውጣ! ውጣ!”
ይህን ሰምቶ መልስ ሲያጣ
ሞት የሚባለው ፈጣጣ
ጭራውን ሸጉቦ ወጣ፡፡

ወይ ጉድ!
ስንቴ በኛ ቂም አርግዞ
ስንቱን ባለቅኔ ወስዶ፣ ስንቱን ቅኔ አግዞ አግዞ፤
“ግጥም ልማር መጣሁ” ይበል? ይሄ ሞት እሚባል ፉዞ
ያውም ከማይጨበጠው፣ ከእሳት አበባው ወዳጄ
ከንጋት ግጥም አዋጄ
ከሞት - ገዳዩ ቀኝ እጄ?
ግን፤
ምን ደስ አለህ አትሉኝም?
ለካ ሞት ግጥም አይችልም
ለካ ሞት ቅኔ አይገባውም!!
የካቲት 27/1998
(ለወዳጄ ለፀጋዬ ገ/መድህን እና ለጥበብ ለቀስተኞች)
/የጋሽ ፀጋዬ አስከሬን ከአሜሪካ መጥቶ፤ ቤቱ ሄጄ በተሰማኝ ስሜት መነሻነት የተፃፈ/ ብሔራዊ ቴያትር በፖለቲካ የግጥም ምሽት ላይ በነሐሴ ልደታ የተነበበ/

Published in የግጥም ጥግ

የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን “የፀረ ሽብር አዋጅና የፓርቲዎች አቋም” በሚል ርዕስ ለዛሬ ቀጠሮ ተይዞለት የነበረውን ክርክር ለሌላ ጊዜ ማስተላለፉ ተቀባይነት የለውም ሲሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ገለፁ። የክርክር ፕሮግራሙ የተራዘመው ለሁለተኛ ጊዜ መሆኑን በመግለፁ ተቃውሟቸውን የገለፁት፣ አንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ (አንድነት)፣ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ መድረክ (መድረክ) እና ሠማያዊ ፓርቲ ናቸው፡፡ በፀረሽብር አዋጅ ዙሪያ ህብረተሰቡ ግልጽ ግንዛቤ እንዲኖረው ማክሰኞ ውይይት ይካሄዳል የሚል የደብዳቤ ጥሪ ደርሷቸው እንደነበር ፓርቲዎቹ አስታውሰው፤ ውይይቱ ወደ ቅዳሜ የተላለፈው አንዳንድ ፓርቲዎች ተጨማሪ የዝግጅት ጊዜ በመጠየቃቸው ነው ተብለን ነበር ብለዋል፡፡ እንደገና በትላንትናው ዕለት ኢቴቪ ውይይቱን ለሁለተኛ ጊዜ አዝራሞታል በማለት ቅሬታቸውን የገለፁት ፓርቲዎቹ፣ በፕሮግራም መደራረብ ምክንያት ውይይቱ ተሰርዞ ለሌላ ቀን እንደተራዘመ የተነገረን በስልክ ነው ብለዋል፡፡ የፕሮግራሙን መሰረዝ አስመልክቶ የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤ ፕሮግራሙ የተሰረዘው “ኢህአዴግ ሃሳብን እንደጦር ስለሚፈራ ነው” ብለዋል፡፡

የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ የአቶ ዳንኤል ተፈራ በበኩላቸው፤ ኢቴቪ ፕሮግራሙን ማራዘሙንም ይሁን መሰረዙን በደብዳቤ እንዳላሳወቀ ጠቅሰው፣ አንድ ሰው ደውሎ ተሰረዘ ወይም ተራዘመ ማለቱ አግባብ ባለመሆኑ አንቀበለውም” ብለዋል፡፡ ለውይይቱ ተወካይ መድበን ነበር የሚሉት የመድረክ ሊ/መንበር አቶ ጥላሁን እንደሻው፤ ለተወካያቸው ተደውሎ ፕሮግራሙ ላልተወሰነ ቀን መራዘሙ እንደተነገራቸው ገልፀዋል፡፡ “የመንግስት ሚዲያዎች ብዙ ጫና እንዳለባቸው እናውቃለን” ያሉት የመድረክ ሊቀመንበር፤ አሁንም ከበላይ አካላት በተላለፈ ክልከላ ፕሮግራሙ ሊሰረዝ እንደቻለ ግምታቸውን ተናግረዋል፡፡

ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር በበኩላቸው፤ የፀረ ሽብር አዋጁ ጉዳይ ይበልጥ ትኩረት ያገኘው አንድነት ፓርቲ “የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት” በሚል አዋጁን ለማሰረዝ እንቅስቃሴ ከጀመረ ወዲህ ነው ብለዋል፡፡ ፓርቲዎችን በደብዳቤ ለውይይት የጋበዙት የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት የዋና ዳይሬክተር ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ ሙላት ገዛኸኝን፣ በስልክ አግኝተናቸው “ምን አይነት መረጃ እንደፈለጋችሁ ከባልደረባዬ ሰምቻለሁ፤ ከ30 ደቂቃ በኋላ ደውሉ፤ አሁን ስራ ላይ ነኝ” የሚል ምላሽ የሰጡን ቢሆንም ከዚያ በኋላ ስልካቸው ስለማይነሳ ሳናገኛቸው ቀርተናል፡፡

Published in ዜና

        የቀድሞ የምድር ጦር ሠራዊት ማህበር፤ የአባላት መዋጮ ታግዶበትና የጡረታ መብት ሳይከበር ለሃያ አመታት በአቤቱታ እንደተንገላታ የገለፁት ም/ዋና ፀሃፊ ኮ/ል አለማየሁ ንጉሴ፤ ማህበሩ እንዲፈርስም ተደርጐብናል ሲሉ አማረሩ፡፡ ለመረዳጃ እድር ከእያንዳንዱ አባል በየወሩ 1 ብር እየተዋጣ የተጠራቀመና በባንክ የተቀመጠ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ያለ አግባብ ታግዶብናል የሚሉት ኮ/ል አለማየሁ፤ ገንዘቡ ከንጉሡ ስርአት ጀምሮ እስከ 1983 ዓ.ም ድረስ፣ በችግርና በሞት ጊዜ ለመረዳዳት ከአባላት ደሞዝ የተዋጣ ነው ብለዋል፡፡ በህጋዊ መንገድ በባንክ የተቀመጠው የእድር ገንዘብ ባልታወቀ ምክንያት ታግዶ ከቆየ በኋላ፣ በፍ/ቤት የክርክር አፈፃፀም ለማህበሩ እንዲለቀቅ ቢታዘዝም ተግባራዊ ሊሆን አልቻለም ብለዋል፤ ኮ/ል አለማየሁ፡፡

ገንዘቡ ለምን አላማ እንደሚውል በባለሙያ አስጠንታችሁ እቅድ አቅርቡ ስለተባልን፣ 7ሺ ብር ከፍለን አስጠንተናል ያሉት ኮ/ል አለማየሁ፤ ለችግረኛ አባላት አገልግሎት የሚሰጥ ክሊኒክና የመዝናኛ ክበብ ለመገንባት እቅድ አውጥተን ብናቀርብም ምላሽ አልተሠጠንም ብለዋል፡፡ በሃገሪቱ ህግ መሠረት ካገለገልንበት መስሪያ ቤት ጡረታ እንዲፈቀድልን ለበርካታ ዓመታት ያቀረብነው አቤቱታ ሰሚ በማጣቱም፣ በኑሮ ውድነቱ እና በሌሎች ጫናዎች የማህበሩ አባላት ህይወት አሳሳቢ እየሆነ መጥቷል ብለዋል፡፡

ምላሽ ሳናገኝ እንድንገላታ መደረጉ፣ የቀድሞ አባቶችን ውለታ መዘንጋት ነው ያሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፣ ይሄ አልበቃ ብሎ ዘንድሮ ማህበሩ ፍቃዱን እንዳያሣድስ ተከልክሏል ብለዋል፡፡ “የቀድሞ የምድር ጦር ሠራዊትና ሲቪል ሠራተኞች ማህበር” የሚለውን ስያሜ ትታችሁ በበጐ አድራጐት ድርጅት ስም ተደራጅታችሁ ኑ ተብለናል ይላሉ - ኮ/ል አለማየሁ፡፡ ማህበሩ ለአመታት ከከተማ አስተዳደር ከንቲባዎች ጀምሮ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር ፅ/ቤት ድረስ በተደጋጋሚ አቤቱታ ቢያደርስም ምላሽ አለማግኘቱን ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

የፕላዝማ የትምህርት ስርጭት ችግሮችን ለማስተካከል የ120 ት/ቤቶች ፕሮጀክት በጨረታ ለዜድቲኢ የተሰጠው ከአመት በፊት ሲሆን፣ በአንድ ት/ቤት በተከናወነ ሙከራ ጭቅጭቅ ስለተፈጠረ ፕሮጀክቱ ተቋረጠ፡፡ በአዲስ ከተማ ት/ቤት የተካሄደው ሙከራ እንዳልተሳካና በእቃዎች ላይ የጥራት ጉድለት እንደሚታይ የገለፁት የትምህርትና ቴክኖሎጂ ማዕከል፣ ዶ/ር ገበየሁ ወርቅነህ፤ የጊዜ ገደቡም ስላለፈ ጨረታውን እንደገና ማውጣት የግድ ነው ብለዋል፡፡ ዜድቲኢ በበኩሉ የጨረታው ህጋዊ አሸናፊ መሆኑን በመጥቀስ፤ በሙከራ ስራውና በእቃዎች ላይ ችግር እንደሌለና ሙሉ ፕሮጀክቱን ለማከናወን እየተጠባበቀ መሆኑን ገልጿል፡፡

መንግስት ለጨረታ የሚያቀርባቸው የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ፕሮጀክቶች ላይ የውጭ ኩባንያዎች ከፍተኛ ተቀናቃኝነት የሚታይባቸው ሲሆን፣ ለመላ አገሪቱ ተመሳሳይ የትምህርት ጥራት ለማዳረስ ያስችላል ተብሎ በከፍተኛ ወጪ የተጀመረው “የፕላዝማ የትምህርት ስርጭት” ፣ በአዲስ አበባ ከሚገኝ ማዕከል በሳተላይት አማካኝነት የተሚላለፍ በመሆኑ ለአስተማሪዎችና ለተማሪዎች አመቺ አልሆነም፡፡ ቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት ስለሆነ፣ በመሃል አስቁሞ አስተማሪው ማብራሪያ የመስጠት እድል የለውም በማለት ጉድለቱን የገለፁት ዶ/ር ገበየሁ፤ተማሪዎች ባይገባቸው ወደኋላ መልሶ መድገም አይቻልም ይላሉ፡፡

የስርጭት ብልሽትና የመብራት መቆራረጥ ካጋጠመም፣ ተማሪዎች ትምህርቱን ሳይከታተሉ ያልፋቸዋል፡፡ በፕላዝማ ቴሌቪዥን የሚቀርበው የቪዲዮ ትምህርት ተማሪዎችና አስተማሪዎች እንዳመቻቸው እንዲቆጣጠሩት ለማድረግም ነው አዲስ የማስተካከያ ፕሮጀክት ተዘጋጅቶ ለጨረታ የቀረበው፡፡ በመጀመሪያው ዙር ለ120 ት/ቤቶች አምና በጥር ወር የወጣውን ጨረታ ያሸነፈው ዜድቲኢ የተሰኘው የቻይና ኩባንያ ሲሆን፣ በአዲስ ከተማ ት/ቤት የሙከራ ውጤት ለማሳየትና በ10 ወራት ውስጥ ሙሉ ፕሮጀክቱን ለማጠናቀቅ ታስቦ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በሙከራው ውጤት ውዝግብ ስለተፈጠረ ፕሮጀክቱ በዚሁ ተቋርጦ ቆሟል፡፡ በቪዲዮ ተቀርፆ ከአንድ ማዕከል በሳተላይት አማካኝነት የሚሰራጨውን ትምህርት የሚቀበል የቪሳት ዲሽ በየትምህርት ቤቱ የተተከለው በቴሌ አማካኝነት እንደሆነ የገለፁት የትምህርትና የቴክኖሎጂ ማዕከል ሃላፊ ዶ/ር ገበየሁ ወርቅነህ በእያንዳንዱ ክፍል ከፕላዝማ ቴሌቪዥን ጋር የሚያገናኝ ኔትዎርክ የተዘረጋው በኛ በኩል ነው ይላሉ፡፡ የፕላዝማ ቴሌቪዥን ስርጭት ለመላ አገሪቱ ተመሳሳይ የትምህርት ጥራት ለማዳረስ የሚረዳ ቢሆንም በቂ እንዳልሆነና ጉድለቶች እንዳሉት እንገነዘባለን ያሉት ዶ/ር ገበየሁ፣ እነዚህን ችግሮች ለማቃለል የተለያዩ ጥረቶችን አድርገናል ብለዋል፡፡

በአስር የትምህርት አይነቶች በፕላዝማ ቴሌቪዥን የሚቀርበውን ትምህርት በሲዲ አዘጋጅተን ለሁሉም ክልሎች ሰጥተናል የሚሉት ዶ/ር ገበየሁ፣ አስተማሪዎች የሲዲ ማጫወቻ ወይም ላፕቶፕ በመጠቀም ከፕላዝማ ቴሌቪዥን ጋር በማገናኘት ለተማሪዎቻቸው ማሳየት ይችላሉ ብለዋል፡፡ ሁነኛው መፍትሔ ግን ለትምህርት ስርጭት የተዘጋጁ ቪዲዮዎችን በሙሉ መያዝና ማከፋፈል የሚችል የኮምፒዩተር ማዕከል በየትምህርት ቤቱ ማቋቋም ነው የሚሉት ዶ/ር ገበየሁ፤ ይህንንም በኔትዎርክ ከእያንዳንዱ ክፍል ጋር ከፕላዝማ ቲቪ ጋር በማገናኘት አስተማሪዎች እንደ አስፈላጊነቱ እየተቆጣጠሩ ለተማሪዎቻቸው ማቅረብ ይችላሉ፡፡ ይህንን የኮምፒዩተር ማዕከልና ኔትዎርክ በየት/ቤቱ ለመዘርጋት በመጀመሪያ ዙር ለ120 ት/ቤቶች የወጣው ጨረታ ዜድቲኢ አሸንፎ ከ200 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት ተመድቦለት እንደነበር ሃላፊው አስታውሰው፤ በአስር ወራት ይጠናቀቃል የተባለው ፕሮጀክት ሳይካሄድ እንደተስተጓጐለ ይገልፃሉ፡፡

በጨረታው ሁለት ደረጃዎች ተጠቅሰዋል የሚሉት ዶ/ር ገበየሁ፤ አንደኛው ነጥብ ለፕሮጀክቱ ትክክለኛውን ጥራት ያሟሉ እቃዎች መቅረባቸውን ማረጋገጥ ነው፤ ሁለተኛው ነጥብ ደግሞ በአንድ ት/ቤት የሙከራ ስራ ተከናውኖ ውጤቱ እንዲታይ ማድረግ ነው ይላሉ፡፡ ለሙከራ በተመረጠው አዲስ ከተማ ት/ቤትም ዜድቲኢ የኮምፒዩተር ማዕከል በማቋቋም ከመማሪያ ክፍሎች ጋር የሚያገናኝ ኔትዎርክ ዘርግቷል፡፡ የሙከራው ውጤት በባለሙያዎቻችን ታይቷል የሚሉት ዶ/ር ገበየሁ፤ በጨረታ ሰነዱ ላይ የተጠቀሱ መመዘኛዎች አያሟላም ብለዋል፡፡ የኮምፒዩተር ማዕከሉና ኔትዎርኩ ሁሉንም የመሣሪያ ክፍሎችን አያዳርስም፤ የእቃዎች ጥራት ችግርም አለበት ይላሉ ዶ/ር ገበየሁ፤ በኛ በኩል ሙከራው እንዳልተሳካና የእቃዎች ጥረት ጉድለት መኖሩን ለሚመለከታቸው አካላት ሪፖርት አቅርበናል፤ ደንቡንና ስርዓቱን ተከትሎ ማድረግ የሚገባቸውን ያደርጋሉ ያሉት ዶ/ር ገበየሁ፤ በፕሮጀክቱ የተያዘው ጊዜ በማለፉና በጀቱ ስለተመለሰ እንደገና ጨረታ ማውጣት የግድ ነው ሲሉም ተናግረዋል፡፡

ይሁን እንጂ ዜድቲኢ 120 ት/ቤቶች በርካታ እቃዎችን ከውጭ አስመጥቶ ማስገባቱንና ከጉምሩክ ለመቀበል ፈቃድ ለማግኘት መቸገሩን ምንጮች ቢገልፁም፤ ዶ/ር ገበየሁ ይሄንን እኛ አናውቅም ብለዋል፡፡ ዜድቲኢ በበኩሉ፣ የጨረታው ህጋዊ አሸናፊ መሆኑንና ካሁን በፊት በርካታ ፕሮጀክቶችን በጥራት እንደሰራ ገልፆ፣ አሁንም በጥራት ሙከራውን እንዳከናወነ ይናገራል፡፡ ስለ ፕሮጀክቱ ለሚነሱ ዝርዝር ጥያቄዎች ምላሽ መስጠት የሚችለው የፕሮጀክቱ ባለቤት ነው የሚለው ዜድቲኢ፣ ሙሉ ፕሮጀክቱን ለማከናወን ዝግጁ ሆኖ እየተጠባበቀ መሆኑን ይገልፃል፡፡

Published in ዜና

የመንግስት ስልጣን ገደብ ቢኖረው ኖሮ ሚኒስትር ዲኤታው ፍ/ቤት ይቆሙ ነበር - ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤ የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ናፍቆት ዮሴፍ “ሰማያዊ ፓርቲ፣ ግንቦት ሰባት እና አክራሪዎች ጋብቻ ፈጽመዋል” በሚል የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ መናገራቸውን የተቃወሙት የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት፤ “የፀረ ሽብር አዋጁ ካልተቀየረ ማንም አይምርም፣ የመንግስት ስልጣን ገደብ ቢኖረው ኖሮ ሚኒስትር ዴኤታው ፍ/ቤት መቆም ነበረባቸው” በማለት ምላሽ ሰጡ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በህዝብ ስም የተቋቋመ ስለሆነ የመንግስት ድክመቶችንና ክፍተቶችን እንዲያስተካክል መታገል ስራው ነው ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ መንግስት የህዝብን ጥያቄ ከመመለስ ይልቅ መፈረጅ ይቀናዋል፤ ይህ ግን ከትግላችን አያግደንም” ብለዋል፡፡

“ከሁለት ወር በፊት የህዝብ ችግሮችና ጥያቄዎች ናቸው ብለን በሰላማዊ ሰልፍ ያሰማናቸው ጥያቄዎች አልተመለሱም” ያሉት ኢ/ር ይልቃል፤ ነሐሴ 26 ቀን 2005 ዓ.ም ሁለተኛውን ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ “ኢትዮጵያ ከአገዛዝ ወደ ዴሞክራሲ ገና አልገባችም፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ገና የስልጣን ባለቤት አልሆነም” ያሉት ኢንጂነሩ፤ እነዚህ ነገሮች እውን እንዲሆኑ በምርጫ ቦርድ ህጋዊ እውቅና አግኝቶ በሰላማዊ መንገድ የሚታገልን ፓርቲ ከአሸባሪዎች ጋር ጋብቻ ፈጽሟል በማለት መወንጀል የአገዛዝ ባህሪ ነው ሲሉ ተችተዋል፡፡ አሸባሪ የሚለው ቃል ትርጉሙን ስቷል የሚሉት ኢ/ር ዘለቀ፤ የፀረ ሽብር አዋጁ እስካልተቀየረ ድረስም ማንንም ከመፈረጅ የሚያግድ ነገር የለውም ብለዋል።

Published in ዜና