ከሁለት ዓመት በፊት በደራሲ ሊዛ ተሾመ ተጽፎ የቀረበው “አሜኬላ ያደማው ፍቅር” ረዥም ልቦለድ መፅሃፍ ተሻሽሎ በድጋሚ ለንባብ በቃ፡፡ “በፍቅር ዓለም በራስ ላይ ማዘዝ ከባድ ነው” የሚለው ልቦለድ መጽሐፍ፤ ለደራሲዋ ሁለተኛዋ ሲሆን ካሁን በፊት “ፍትህን በራሴ” የተሰኘ መጽሐፍ ለንባብ አብቅታለች፡፡ 268 ገፆች ያሉት መጽሐፉ፤ በኢንተርናሽናል ሊደርሺፕ ኢንስቲትዩት ማተሚያ ቤት የታተመ ሲሆን ለሀገር ውስጥ ገበያ 45.60 ብር፣ ለውጭ ገበያ ደግሞ 10 ዶላር ይሸጣል፡፡

በአንተነህ ግርማ ተጽፎ ተካበ ታዲዮስ ያዘጋጀውና በካም ግሎባል ፒክቸርስ የቀረበው “አማረኝ” ፊልም የፊታችን ሰኞ ከምሽቱ 12 ሰዓት ብሔራዊ ትያትር እንደሚመረቅ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ የ103 ደቂቃ ርዝመት ያለው ፊልሙ፤ በአራት ወራት ተሰርቶ የተጠናቀቀ ሲሆን ዮሐንስ ተፈራ፣ አማኑዔል ሀብታሙ፣ ባዩሽ ከበደ፣ ካሳሁን ፍስሃ (ማንዴላ) እና ሌሎችም ተውነውበታል፡፡ በሥራ እና በትዳር ጫና ሳቢያ እረፍት በፈለገ ወጣት ታሪክ ላይ የተሰራው ፊልም፤ ከሰኞው ዋና ምርቃት በፊት አዲስ አበባ በሚገኙት ኤድናሞል፣ አለም፣ ዋፋ፣ እምቢልታ፣ አጐና እና ኢዮሃ ሲኒማ ነገ ከቀኑ 8፣ 10 እና 12 ሰዓት ለሕዝብ እይታ ይበቃል፡፡
ካም ግሎባል ፒክቸርስ ቀደም ሲል “ስውሩ እስረኛ”፣ “በራሪ ልቦች”፣ “አማላዩ”፣ “ሼፉ” እና “ወደገደለው” የተሰኙ ፊልሞችን ለእይታ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በ3ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ደቡብ አፍሪካ ላይ ሲሳተፍ በዚያው አገር በሚኖሩ ስደተኛ ኢትዮጵያውያን ድጋፍ ከፍተኛ ትኩረት እንደሚያገኝ ተጠብቋል፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ለምትሳተፍበት የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ CHAN ውድድር ያለፈው ከሳምንት በፊት በኪጋሊ ከተማ የሩዋንዳ አቻውን በመለያ ምት 5ለ6 በሆነ ውጤት በማሸነፉ ነው፡፡
የመጀመርያው ተሳትፎ በቻን
በ2014 እኤአ መግቢያ ለሚጀመረው 3ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ 12 አገራት ከወዲሁ ማለፋቸውን አረጋግጠዋል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ፤ ሊቢያ እና ጋና በቀጥታ ማለፋቸውን ሲያረጋገጡ ፤ ከመካከለኛውና ምስራቅ አፍሪካ ዞን ኢትዮጵያ፣ ብሩንዲ እና ኡጋንዳ፤ ከሰሜን አፍሪካ ዞን ሞሮኮ ፤ ከማእከላዊ አፍሪካ ዞን ኮንጎ፤ ከምእራብ አፍሪካ ዞን ናይጄርያ፣ ቡርኪናፋሶ፣ ሞውታንያና ማሊ በመጨረሻ ዙር የማጣርያ ውድድር ያለፉት ሌሎቹ 9 አገራት ናቸው፡፡ በ2010 እኤአ ላይ 19ኛውን የዓለም ዋንጫ እንዲሁም በ2013 እኤአ ላይ 29ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ያዘጋጀችው ደቡብ አፍሪካ በ2014 እኤአ ላይ 3ኛውን የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ በተሳካ ሁኔታ ለማስተናገድ ፍላጎት እንዳላት የውድድሩ አዘጋጆች ከሰሞኑ ተናግረዋል፡፡ 29ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ደቡብ አፍሪካ ባስተናገደችበት ወቅት ስርዓቱን በሳተ የትኬት አሻሻጥና በስታድዬም ተመልካች ድርቅ የዝግጅት ድክመት ቢታይም ከውድድሩ እስከ 7.2 ሚሊዮን ብር ማትረፍ ተችሏል፡፡
የአገሪቱ እግር ኳስ ፌደሬሽን በ3ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ደማቅ መስተንግዶ ለማድረግ 50 በመቶ ዝግጅቱን እንዳጠናቀቀም ገልጿል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ለዚሁ ውድድር በአራት ከተሞቿ የሚገኙ ስታድዬሞችን አዘጋጅታለች፡፡ የውድድሩን የመክፈቻ እና የመዝጊያ ጨዋታ የምታስተናግደው ኬፕ ታውን 64100 ተመልካች በሚይዘው የኬፕታውን ስታድዬም ፤ ፖልክዎኔ ከ1ሺ በላይ ተመልካች በሚይዘው የፒተር ሞኮባ ስታድዬም ፤ ብሎምፎንቴን እስከ 41ሺ ተመልካች በሚይዘው የፍሪስቴት ስታድዬም እና ኪምበርሌይ 18ሺ ተመልካች በሚያስተናግደው የሆፌ ፓርክ ስታድዬም የቻን ጨዋታዎችን ያስተናግዳሉ፡፡
በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን አማካኝነት የተመሰረተው ሻምፒዮናው በየአገሩ ሊጎች በመጫወት ለፕሮፌሽናል እድል ለመብቃት ያልቻሉ ተጨዋቾችን ወደ ገበያ ለማውጣት፤ የክለቦችን አህጉራዊ አስተዋፅኦ ለማሳደግ፤ የየአገራቱን የሊግ ውድድሮች ደረጃ እና የፉክክር ብቃት ለማጠናከር እንዲሁም በዋናው የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር መሳተፍ ለማይሆንላቸው የአህጉሪቱ ቡድኖች የውድድር እድል ለመፍጠር አመቺ መድረክ መሆኑ ይገለፃል፡፡
የስደተኞቹ ኢትዮጵያውያን ድጋፍ
ዋልያዎቹ የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ወይም ቻን ላይ በሚኖራቸው ተሳትፎ በደቡብ አፍሪካ በሚኖሩ ስደተኛ ኢትዮጵያውያን አስደናቂ ድጋፍ ስለሚገኙ ከፍተኛ ትኩረት መሳባቸው የማይቀር ነው፡፡ 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በደቡብ አፍሪካ በተካሄደበት ወቅት ስደተኛ ኢትዮጵያውያን ለዋልያዎቹ 12ኛ ተጨዋቾች እንደነበሩ የሚታወስ ነው፡፡ በዋና ከተማዋ ጆሃንስበርግ እንዲሁም ዋልያዎቹ የምድብ 3 ግጥሚያዎችን ባደረጉባቸው በኔልስፑሪቱ ሞምቤላ ስታዲየም እና በሩስተንበርጉ ሮያል ባፎኬንግ ስታድዬም በ50 ሺዎች የሚገመቱ ስደተኛ ኢትዮጵያውያን ለአፍሪካ ዋንጫው ከፍተኛ ድምቀት ማላበሳቸው አይዘነጋም፡፡ በስደት፤ በትምህርት እና በስራ በደቡብ አፍሪካ የተለያዩ ግዛቶች የከተሙት ኢትዮጵያውያን በፍፁም የአገር ፍቅር መንፈስ እና አንድነት ለቡድናቸው ከፍተኛ ድጋፍ ማድረጋቸው ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የቻን ውድድር ውጤታማነት ከፍተኛ አስተዋፅጽኦ እንደሚኖረው ይጠበቃል፡፡
ከአፍሪካ ዋንጫ ወደ ቻን ከዚያም ወደዓለም ዋንጫ…
በሌላ ዜና የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በደቡብ አፍሪካ በ2014 ለሚዘጋጀው 3ኛው የአፍሪካ ሻምፒዮና ውድድር ማለፉን ካረጋገጠ በኋላ ለእረፍት የተበተነ ሲሆን ከ6 ሳምንታት በኋላ ለዓለም ዋንጫ የመጨረሻ የጥሎ ማለፍ ማጣርያ ለማለፍ በምድብ 1 የ6ኛ ዙር ወሳኝ ጨዋታ ከመካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ ጋር ይገናኛል፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን እና ፊፋ ይህ ወሳኝ ጨዋታ በኮንጎ ዋና ከተማ ብራዛቪል እንዲደረግ ሲወስኑ፤ ውድድሩን የሚመሩት ዳኞች ከአልጄርያ መመደባቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በ5ኛ ዙር የምድብ ማጣርያ ጨዋታዎች ለመጨረሻው የጥሎ ማለፍ ማለፍ ትንቅንቅ ማለፋቸውን ያረጋገጡት 3 አገራት ኮትዲቯር ፤ ግብፅ እና አልጄርያ ናቸው በቀሪዎቹ ሰባት ምድቦች ምድባቸውን በመሪነት የሚያልፉትን ለመለየት የስድስተኛ ዙር የምድብ ማጣርያ ጨዋታዎች ይጠበቃሉ፡፡
ኢትዮጵያ በፊፋ ተገቢ ያልሆነ ተጨዋች በማሰለፍ ምክንያት በቅጣት ሶስት ነጥብ ከተቀነሰባት በኋላ ምድብ አንድን በ5 ጨዋታዎች ባስመዘገበችው 10 ነጥብ እና 1 የግብ ክፍያ ስትመራ፤ ደቡብ አፍሪካ በ8 ነጥብ እና በ4 የግብ ክፍያ፤ ቦትስዋና በ7 ነጥብ እና በ1 የግብ ክፍያ እንዲሁም ሴንተራል እፈሪካ ሪፖብሊክ በ3 ነጥብ እና በ6 የግብ እዳ እስከ አራት ያለውን ደረጃ አከታትለው ይዘዋል፡፡
በምድቡ የ6ኛ ዙር የመጨረሻ ጨዋታዎቻቸው ሴንተራል አፍሪካ ሪፖብሊክ እና ኢትዮጵያ በገለልተኛ ሜዳ ኮንጎ ብራዛቪል ላይ ሲጫወቱ፤ ደቡብ አፍሪካ ደግሞ በሜዳዋ ቦትስዋናን ታስተናግዳለች፡፡ በተመሳሳይ ቀን በተመሳሳይ ሰዓት በሚደረጉት ሁለት ጨዋታዎች በሚመዘገቡ ውጤቶች ኢትዮጵያ ካሸነፈች ብቻ በቀጥታ ለጥሎ ማለፉ ማጣርያ ማለፏን ታረጋግጣለች፡፡
ደቡብ አፍሪካ እና ቦትስዋና በበኩላቸው በመሸናነፍ፤ ከዚያም የኢትዮጵያ ነጥብ መጣል በመጠበቅ በያዙት የግብ ክፍያ ብልጫ ለማለፍ ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ የጎል ድረገፅ አንባቢዎች በሰጡት የውጤት ትንበያ ኢትዮጵያ ምድቡን በመሪነት እንደምታጠናቅቅ ተመልክቷል፡፡
በኮንጎ ብራዛቪል በሚደረገው ጨዋታ ኢትዮጵያ ሴንተራል አፍሪካን 31.77 በመቶው 3ለ1፤ 15.29 በመቶው 2ለ1 እንዲሁም 12.94 በመቶው 2ለ0 ታሸንፋለች ብለው ገምተዋል፡፡ በሌላው የምድቡ ጨዋታ ደግሞ ደቡብ አፍሪካ ቦትስዋናን 21.05 በመቶው 2ለ0 እንዲሁም 15.79 በመቶው 3ለ1 እንደምታሸንፍ ሲተነብዩ ያህሉ አንድ እኩል አቻ ይለያያሉ በሚል ገምተዋል፡፡
የዋልያዎቹ ዋጋ መጨመር
ይህ በእንዲህ እንዳለ በዚህ ትውልድ ያሉት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ዘንድሮ በእግር ኳስ ታሪክ ከፍተኛውን ውጤት በማስመዝገብ ላይ መሆናቸውን የተለያዩ ሁኔታዎች እያመለከቱ ናቸው፡፡
ዋልያዎቹ ኢትዮጵያ ለ31 አመታት የራቀችበትን ታሪክ በመቀየር ለ29ኛው አፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ ካበቁ በኋላ ለአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ የመጀመርያ ተሳትፎ የደረሱ ሲሆን አገራችን በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ለዓለም ዋንጫ ተሳትፎ ለምትበቃበት እድል ከፍተኛ የውጤት ተስፋ ይዘው ይገኛሉ፡፡ በዚሁ ታሪክ ሰሪ ትውልድ ሳቢያም በትራንስፈር ማርኬት በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የዝውውር ገበያ የዋጋ ግምት ላይ ጭማሪ እየታየም ነው፡፡ ከወር በፊት በአጠቃላይ ስብስቡ በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመን 725ሺ ዩሮ የነበረው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እስከ 1 ሚሊዮን ዩሮ በመተመን ግምቱ ጨምሯል፡፡
ለዚህም አራት የብሄራዊ ቡድኑ ተጨዋቾች ወደ ተለያዩ አገራት ክለቦች ዝውውር መፈፀማቸው ምክንያት ነው፡፡
ምንም እንኳን በትራንስፈርማርከት ድረገፅ የጌታነህ ዝውውር ሂሳብ እንደ አዲስ ተጨምሮ ብሄራዊ ቡድኑ በ875ሺ መተመኑ ቢገለፅም ወደ እስራኤል ክለብ አይሮኒ ኒር ራማት ሃሻሮን የሄደው አስራት መገርሳ 37.88 ሺ ዩሮ፤ ወደ ሊቢያው ክለብ አልኢትሃድ የሄደው ሽመልስ በቀለ 128.79 ሺ ዩሮ እና ወደ ሱዳን ክለብ አልሃሊ ሼንዲ የሄደው አዲስ ህንፃ 30.23 ሺ ዩሮ የዝውውር ሂሳብ በዝርዝር በትራንስፈርማርከት ውስጥ ሲገባ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የዋጋ ተመን ከ1 ሚሊዮን ዩሮ በላይ መሆኑ አይቀርም፡፡

 

በ10ኛው የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ ቅዱስ ጊዮርጊስ የምድብ አንድን መሪነት ለማጠናከር በሁለት ሳምንት ልዩነት ከሁለት የቱኒዚያ ክለቦች ጋር ከሜዳው ውጭ ሊፋለም ነው፡፡ የጎል ድረገፅ አንባቢዎች በጨዋታው ላይ በሰጡት የውጤት ትንበያ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ውጤታማነት ያደሉ ግምቶችን ሰንዝረዋል፡፡ ጊዮርጊስ ከሜዳው ውጭ ከኤትዋል ደ ሳህል ጋር በሚያደርገው ጨዋታ 40 በመቶው 1ለ0 እንዲሁም 20 በመቶው 2ለ0 እንደሚያሸንፍ ሲገም/ ቀሪዎቹ 20 በመቶ ብቻ 3ለ1 እንደሚሸለፍ ተንብየዋል፡፡
በምድብ አንድ የመጀመርያ ጨዋታው ቅዱስ ጊዮርጊስ የማሊውን ክለብ ስታድ ዴማሊዬን ከ2 ሳምንት በፊት በአዲስ አበባ ስታድዬም በኡመድ ኡክሪ እና ፍፁም ገብረማርያም ጎሎች 2ለ0 ማሸነፉ አይዘነጋም፡፡
ከዚህ ጨዋታ በፊት የጊዮርጊስ ምክትል አሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝ ከካፍ ኦንላይን ድረገፅ ጋር ባደረገው ቃለምምልስ በምድብ ጨዋታዎች የመጀመርያ ጨዋታን ማሸነፍ በቀጣይ ለሚኖር ውጤታማነት ወሳኝ እንደሆነ ተናግሮ ነበር፡፡ ከምድብ ማጣርያው የመጀመርያ ጨዋታዎች በኋላ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ3 ነጥብ እና በሁለት የግብ ክፍያ ምድብ አንድን ይመራል፡፡ የቱኒዚያው ክለብ ሲኤስ ኤስፋክስዬን ሌላውን የአገሩን ክለብ ኤትዋል ደ ሳህል በመጀመርያ ጨዋታ 1ለ0 በማሸነፉ በ3 ነጥብ እና በ1 የግብ ክፍያ ሁለተኛ ነው፡፡
ኤትዋል ደሳህል ያለምንም ነጥብ በ1 የግብ እዳ እንዲሁም የማሊው ስታድ ዴማሊዬን ያለምንም ነጥብ በሁለት የግብ እዳ 3ኛ እና 4ኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡
በ10ኛው የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ ምድብ ሁለት ደግሞ ሁሉም ክለቦች በመጀመርያ ጨዋታቸው አቻ ውጤት በማስመዝገባቸው በ1 ነጥብ ያለምንም ግብ እዳ ከ1 እስከ 4 ያለውን ደረጃ ተጋርተውታል፡፡ በዚሁ ምድብ የመጀመርያ ዙር ጨዋታዎች የሞሮኮው ኤፍዩኤስ ራባት ከቱኒዚያው ቢዜርቴን እንዲሁም የአልጄርያው ኢኤስ ሴቲፍ ከዲ.ኮንጎው ቲፒ ማዜምቤ በተመሳይ 1ለ1 አቻ ተለያይተዋል፡፡
ቅዱስ ጊዮርጊስ ከኤትዋልደሳህል ጋር ዛሬ ለሚያደርገው የምድቡ ሁለተኛ ጨዋታ ከትናንት በስቲያ ወደ ቱኒዚያ የተጓዘ ከሳምንት በኋላም ወደዚያው በመመለስ የምድቡን 3ኛ ዙር ጨዋታ ከሴፋክስን እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡ ከእነዚህ ሁለት ወሳኝ ጨዋታዎች በኋላ በአራተኛ ዙር የምድቡ ጨዋታ አዲስ አበባ ላይ የቱኒዚያውን ኤትዋል ደሳህልን ይገጥምና ወደ ማሊ በመጓዝ ከስታድ ዴማሊዬን ጋር የምድቡን 5ኛ ዙር ጨዋታ አድርጎ በመጨረሻም ሴፋክስን አዲስ አበባ ላይ በ6ኛ ዙር ጨዋታው በማስተናገድ የምድብ ጨዋታውን ያጠናቅቃል፡፡
በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ሱፕር ስፖርት እንደዘገበው በቱኒዚያ ከሰሞኑ በተፈጠረው ሁከት ሳቢያ በአፍሪካ ደረጃ በውድድር ላይ የሚገኙ የአገሪቱ ክለቦች በሜዳቸው የሚያደርጓቸውን ግጥሚያዎች ላልተወሰነ ጊዜ በዝግ ስታድዬም እንዲያካሂዱ መንግስት እንደወሰነ ነው፡፡ የቱኒዚያ ክለቦች በዚሁ ውሳኔ ላይ አቋማቸውን እስከትናንት ያልገለፁ ቢሆንም ውሳኔው የክለቦቹን ውጤታማነት ሊጎዳ እንደሚችል እና እግር ኳስ አፍቃሪ በሆኑ ደጋፊዎቻቸው ላይ መጥፎ ስሜት መፍጠሩ እንደማይቀር በሱፕር ስፖርት ዘገባ ተገልጿል፡፡ ሁለቱ የቱኒዚያ ክለቦች በአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ ውጤታማነት የሚታወቁ የሰሜን አፍሪካ ክለቦች ሲሆኑ ኤትዋል ደሳህል 1 ጊዜ እና ሲኤስ ሴፋክሴዬን ለ2 ጊዜያት ዋንጫውን የወሰዱ ናቸው፡፡
41 ተጨዋቾች የሚገኙበት የኤትዋል ደሳህል ስብስብ 10 የሌላ አገር ዜግነት ያላቸው ፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ሲገኙበት ቡድኑ በትራንስፈርማርኬት የዝውውር ገበያ ተመን መሰረት 11.53 ሚሊዮን ዩሮ እንደሚያወጣ ሲገመት ሌላው የአገሪቱ ክለብ ሲኤስ ሴፋክሲዬን 3 የውጭ ዜግነት ያላቸውን ተጨዋቾችን ጨምሮ በቡድኑ 25 ተጨዋቾች አስመዝግቦ 6.8 ሚሊዮን ዩሮ የተተመነ ነው፡፡ የማሊው ክለብ ስታድ ዴ ማሊዬን 2 የውጭ ዜግነት ያላቸውን ተጨዋቾችን ጨምሮ በቡድኑ 39 ተጨዋቾች አስመዝግቦ በትራንስፈርማርኬት የዝውውር ገበያ ተመን 650ሺሮ ሲገመት፤ የኢትዮጵያው ቅዱስ ጊዮርጊስ 5 የውጭ ዜግነት ያላቸውን ተጨዋቾችን ጨምሮ በቡድኑ 26 ተጨዋቾች ያስመዘገበው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ125ሺ ዩሮ ተተምኗል፡፡

 

Saturday, 03 August 2013 11:03

“…የወንዶች መካንነት…”

ቀደም ያሉ ጥናቶች እንደሚያሳዩት ለዘር መካንነት የሚበቁ ወንዶች ችግር ከአእምሮ ጋር የተገናኘ መሆኑን የሚያመላክት ሲሆን በቅርብ የወጡት ደግሞ 90% የሚሆኑት ምክንያቶች የተፈጥሮ ወይንም አካላዊ ችግሮች መሆናቸውን ይገልጻሉ ፡፡ ቢሆንም ግን ከአካላዊ ችግር የተነሳ መውለድ ያቃታቸውም ቢሆኑ ሁኔታው በመከሰቱ እራሳቸውን ዝቅ አድርገው መመልከት፣ መበሳጨት፣ እራስን እንደጥፋተኛ የመቁጠር ሁኔታዎች ስለሚታይባቸው የአእምሮ ወይንም የአስተሳሰብ ችግርም ይገጥማቸዋል፡፡ ወንዶች ለመካንነት ያላቸው ድርሻ ምን ያህል ነው? የሚለውን በዚህ እትም ለንባብ ያልን ሲሆን ማብራሪያውን የሚሰጡት ዶ/ር እስክንድር ከበደ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ትምህርት ቤትጥቁር አንበሳ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትና መምህር ናቸው።
ጥ/ መካንነት እንዴት ይገለጻል?
መ/ መካንነት ማለት ጥንዶች ለአንድ አመት ያህል አብረው እየኖሩ ነገር ግን ሴቲቱ ልጅ ማርገዝ ካልቻለች የመካንት ችግር አለ ብሎ መደምደም ይቻላል፡፡ ይህ አገላለጽ የሚጠቅመው ጥንዶች አብረው እየኖሩ ልጅ መውለድ አልቻልንም ብለው ምክንያቱን ሊያስቡና ወደሕክምና ሄደውም መፍትሄውን መጠየቅ የሚችሉበትን ጊዜ ለመጠቆም እንዲረዳ ነው፡፡ በእርግጥ ይህንን ጊዜ በእድሜ ልዩነት ከፋፍሎ መመልከት ያስፈልጋል፡፡ ተጋቢዎቹ ወጣት ከሆኑ እስከ አንድ አመት ሁኔታውን በትእግስት መከታተል ሲገባ ነገር ግን ሴቲቱ ከ35/አመት በላይ ከሆነች እስከአንድ አመትም መታገስ ሳያስፈልግ ቀደም ብሎ መከታተል ይገባል፡፡
ጥ/ ለመካንነት የወንዶች ድርሻ ምን ያህል ነው?
መ/ ቀደም ባሉት ጊዜያት ጥንዶች ልጅ መውለድ ካልቻሉ መካን የሆነችው ሴትዋ ነች እንጂ የወንድ መካን የለም ብለው ያምኑ ነበር፡፡ ይህ ግን የተሳሳተ አመለካከት ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ በአለው የሳይንስ እድገት እንደተረጋገጠው ከሆነ በጥንዶች መካከል ለመካንነት የወንዶች ተሰትፎ ወደ 20% ይሆናል፡፡ በእርግጥ በሴትዋም በወንዱም በኩል ልጅ ያለማግኘት ችግር ሲከሰት ለምክንያትነቱ ከ20-40% ያህል ወንዶች ናቸው።
ጥ/ ለወንዶች መካንነት ምክንያቱ ምንድነው?
መ/ ወንዶች መካን ሆኑ ሲባል በአራት ሊከፈል ይችላል፡፡
በጭንቅላት አካባቢ የሚፈጠሩ ችግሮች (1-2%)
ፒቱታሪ ግላንድ ላይ ስራቸውን የሚሰሩ ሆርሞኖች ማነስ ፣የፒቱታሪ ግላንድ እጢዎች መኖር ፣በተለያዩ ሕመሞች ምክንያት የሚወሰዱ አንዳንድ መድሀኒቶች ፣በተለያዩ ምክንያቶች በጭንቅላት ላይ የሚደርሱ አደጋዎች፣ እንደ ቲቢ ፣የስኩዋር በሽታ ያሉ አድካሚ በሽታዎች ፣መነንጃይትስ የመሳሰሉ ለኢንፌክሽን የሚያጋልጡ ሕመሞች፣ ከመጠን በላይ ውፍረት መካንነትን በወንዶች ላይ ሊያስከትል ይችላል፡፡
በዘር ፍሬ ማምረቻ Testis ላይ የሚፈጠር ችግር (30-40%)
የዘር ማመንጫ ወይንም ማስቋሽቋ የሚ ባለው የሰውነት ክፍል በትክክለኛው አፈጣጠር 46/ ክሮሞዞም ሊኖረው ሲገባ ነገር ግን አንድ ተጨማሪ ማለትም 47/ክሮሞዞም ቢኖራቸው ሙሉ በሙሉ መካን ያደርጋል፡፡
ወንድ ሲፈጠር የዘር ማመንጫው የሚገኘው በሆድ ውስጥ ነው፡፡ ነገር ግን ቀስ በቀስ ወደ ትክክለኛው ቦታው የሚመጣ ይሆናል፡፡ ልጁ ከተወለደ ከአንድ አመት በላይ የዘር ማመንጫው በተፈጠረበት ሆድ እቃ ውስጥ ከቆየ የመካንነት ችግር ሊያጋጥም ይችላልዶ/ር እስክንድር ከበደ ከመካንነት ባለፈም የካንሰር ችግርም ሊያጋጥም ይችላል፡፡ ስለዚህም በጊዜው በኦፕራ ሲዮን መስተካከል ይገባዋል፡፡
የደም መልስ ቡዋንቡዋዎች መስፋት የወንድ ዘርፍሬ ማመንጫ አካባቢ ሙቀት በመፍጠር ትክክለኛ የሆነ የስፐርም አፈጣጠር ሂደት እንዳይኖር ያደርጋል። ጆሮ ደግፍ የሚባል በሽታ ወንዶ በእድሜያቸው ከጉርምስና በሁዋላ ሲደርሱ ከታመሙ ወደ 25% የሚሆኑት የዘር ማመንጫ ፍሬውን ስለሚጎዱ መካንነትን ሊያስከትል ይችላል፡፡ በአብዛኛው ግን ጆሮ ደግፍ በሽታ በልጅነት ስለሚይዝ ለዚህ ችግር ብዙዎችን አይዳርግም፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የስጋ ደዌ በሽታ በልጅነት እድሜ ከያዘ እንዲሁም ቲቢ የተባለው በሽታ በጊዜው ካልታከመ ለወንዶች የመካንነት ችግርን ሊያስከትል ይችላል፡፡ ለካንሰር የሚወሰዱ መድሀኒቶች፣ የጨረር ሕክምና በዘር ፍሬ ማምረቻው ከተወሰነ መጠን በላይ ካረፈ የዘር ፍሬውን ስለሚያበላሽ መካን ያደርጋል፡፡ የኩላሊት ወይንም የጉበት በሽታ እንዲሁም ካንሰር ከመጨረሻው ደረጃ ላይ ከደረሱ የወንድ የዘር ፍሬ ውጤታማ እንዳይሆን ስለሚያደርጉ መካንትን ያስከትላሉ፡፡
ስፐርም ከተመረተ በሁዋላ ወደውጭ እንዲፈስ ባለው አካሄድ መስመሩ ወይንም
መጉዋጉዋዣው ሲዘጋ (20-30%)
እስፐርም ከተመረተ በሁዋላ ወደሴቷ እንቁላል በመጉዋዝ ልጅ እንዲመረት የሚያደ ርገው መስመር በተለምዶው የትራንስፖርት መስመር ይባላል። ይህ መስመር ማለትም የዘር ማስተላለፊያው ቱቦ በኢንፌክሽን ወይንም ቀደም ብሎ ባጋጠመ እንደ ጨብጥ ባሉ በተለያዩ በሽታዎች ምክንያት መስመሩ ከተዘጋ አለዚያም በተፈጥሮ ምክንያት ቱቦው እስከጭርሱንም ላይፈጠር ስለሚችል እንደ አንድ ችግር ሊቆጠር የሚችል ነው፡፡
ምክንያቱ የማይታወቅ (ከ40-50%)
በተለያዩ የአኑዋኑዋር ሁኔታዎች ማለትም ሲጋራ ማጨስ፣ የአደንዛዥ እጾችን መውሰድ፣ አልኮሆል በከፍተኛ ሁኔታ መውሰድ፣ ከባድና ተከታታይ የሆነ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማድረግ፣ በጣም ጠባብ የሆነ የውስጥ ሱሪ መልበስ፣ የአካባቢ አየርን መበከል ለሚችሉ መርዛማ ኬሚካሎች መጋለጥ፣ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት፣ ከፍተኛ ጭንቀት ...ወዘተ አንድን ወንድ ለመካንነት ሊዳርጉ ከሚችሉ መካከል ናቸው፡፡
ጥ/ ሕክምና አለው?
መ/ ሕክምና አለው፡፡ ሕክምና ሲባል ግን መጀመሪያ ጥንዶቹ መካንነትን ለማረጋገጥ በጋራ
ከሐኪሙ ጋ ሲቀርቡ የሚጀመር ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ ጥንዶች ልጅ ማግኘት ካልቻሉ ተፈጥሮአዊውም ይሁን ሰው ሰራሹ ችግሩ ከሴትዋ ይሆናል የሚል ግምት በመያዝ ወንዶቹ ሐኪም ጋ አይቀርቡም፡፡ ሴቶቹ ብቻ ምርመራ በማድረጋቸው የሚገኘው ውጤት አመርቂ አይሆንም፡፡ ስለሆነም ጥንዶች በጋር ምርመራ ሲጀምሩ መጀመሪያ ዝርዝር የሆነውን ታሪካቸውን በመውሰድ በተለይም ወንዶቹን በሚመለከት፡-
የዘርፍሬው አፈጣጠር እና ያሉበት ቦታ ትክክለኛ ነው አይደለም ?
ቫሪኮስ የሚባለው ማለትም የደም ስሮቹ የመስፋት ሁኔታ ይታይባቸዋል ወይ?
ቱቦው በትክክል ተፈጥሮአል ወይ?
ሰውየው ትክክለኛ የሆነ ወሲባዊ እንቅስቃሴ አለው የለውም? ...ወዘተ
ከላይ የተመለከቱት ጥያቄዎች ባካተተ ሁኔታ በምርመራ ከተረጋገጠ በሁዋላ ፈሳሹ ተወስዶ ምርመራው ይቀጥላል፡፡ በዚህም ከወንዱ የሚወጣው ዘር መጠን ትክክለኛነት እንዲሁም አሲድ አለው የለውም? ቅጥነቱ ፣ውፍረቱ ፣የስፐርም ቁጥሩ እንዲሁም በአንድ ጊዜ በሚወጣው ፈሳሽ ውስጥ ምን ያህል ስፐርም አለ? እንቅስቃሴያቸውና አፈጣጠራቸው ትክክል ነው ወይ? የሚለው ባጣቃላይም የአለም የጤና ድርጅት ባስቀመጠው መስፈርት መሰረት ታይቶ ጥሩ ውጤት ካለው ወንድየው የመካንነት ችግር እንደሌለበት ምስክርነት ሊሰጠው ይችላል፡፡ ነገር ግን ውጤቱ ጥሩ ካልሆነ ምርመራው በአንድ ጊዜ አጋጣሚ የተደረገ በመሆኑና ምናልባትም ለቀጣይ የሚሻሻልበት ሁኔታ ስለሚኖር እንደገና ከአንድ ወር በሁዋላ ለምርመራ ይቀጠራል፡፡ ይህ ሁሉ ምርመራ ከተደረገ በሁዋላ እንደሁኔታው በህክምና የሚድንም የማይድንም ይኖራል፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

“መልክአ-ስብሐት” የተሰኘውን እና በደራሲ ስብሐት ገ/እግዚአብሔር ህይወት እና ሥራ ዙሪያ የሚያጠነጥነውን ሰሞነኛ መፅሐፍ በትኩሱ አንብቤ ከመጨረሴ በውስጡ ፍንትው እና ቦግ ያለ አርእስት የያዘ አንድ መጣጥፍ ላይ አስተያየት ብጤ ለመከተብ ልቤ ተጣደፈ፡፡ የመጣጥፉ ርዕስ “ስብሐት ገ/እግዚአብሔርን ከሌላ ማዕዘን” ይላል፡፡ የጥድፊያዬ ምክንያት ባለመጣጥፉ አቶ ሚካኤል ሽፈራው፤ ማንኛውንም “ከስሜት ነፃ” የሆነ አስተያየት ለማስተናገድ ክፍት እንደሆኑ በቅድምያ በማሳወቅ ያቀረቡት ግብዣ ነው፡፡ ታዲያ በእንዲህ አይነቱ ልባዊ ግብዣ ልቡ ወከክ የማይል ማን አለ? በተለይ ደግሞ ሙሉ በመሉ ባይሆንም ከእርሳቸው ጋር የሚጋራው ሀሳብ ያለው እንደኔ አይነቱ ሰው! በፀሐፊው ልበሙሉነት እና ተጋፋጭነት ያደረብኝ አድናቆትም የራሱን ድርሻ አዋጥቷል፡፡ እስኪሰለቸን ድረስ በየጋዜጣውና በየመፅሔቱ ስለ ስብሐት አንድ አይነት መወድስ በምንሰማበት ወቅት አለአንዳች ፍርሃት እና ማመንታት የሚሰማቸውን እና የሚያስቡትን የገለጡበት ሁኔታ ያስቀናል፡፡
ብዕር እንዳነሳ ያጣደፉኝ እኒህ ቢሆኑም የፅሁፌ ዓላማ ግን ወዲህ ነወ፡፡

አቶ ሚካኤል የስብሐትን ህይወትና ሥራ ፋይዳ ለማጣጣል እና ለማንኳሰስ የተጠቀሙባቸው ማስረጃዎች አንድም ደካማ አንድም ደግሞ ተጣራሽ ሆነው በማግኘቴ እነዚህን ህፀፆች በተቻለ መጠን በመልቀም ለእሳቸውም ሆነ በስብሐት ላይ ተመሳሳይ ከሆነ “ሌላ ማዕዘን” ለመፃፍ ምኞቱ ላላቸው ጠንከር ያለ ፅሑፍ እንዲፅፉ ለማበረታታት ነው፡፡ ምክንያቱም እኔም ራሴ ምድቤ ስብሐትን በስስት ከሚያዩት ሳይሆን የጐሪጥ ከሚያዩት መካከል ነኝና፡፡ ሦስተኞቹ ቡድኖች የሚያጉረጠርጡበት ናቸው፡፡ ከእነርሱ የለሁበትም፡፡ የአቶ ሚካኤል ፅሁፍ ድካም፣ ስብሐት እና ስብሐታዊ ትኩሳቱ ላይ ቀዝቃዛ ውሃ ለመቸለስ የሚቋምጡ ሁሉ አስቀድመው የባልዲያቸውን ሽንቁር መድፈን እንደሚበጃቸው የሚያስተምር ይመስለኛል፡፡
አንድ… ሁለት እያለ እስከ ሃያ በሚደርሱ (በቆጠራ ስህተት አስራ ዘጠኝ ተብለው ተቆጥረዋል) ንዑስ አርእስቶች የተከፋፈለው የአቶ ሚካኤል ፅሁፍ ውስጥ አምስት ያህሉ በስብሐት የግል ባህሪይ ላይ የሚያተኩሩ፣ አራት ያህሉ ፀሐፊው ከስብሐት ጋር ባሳለፈው ዘመን የገጠመውን የግል ተሞክሮ የሚያትቱ ሲሆን የተቀሩት ደግሞ ፀሐፊው የአቶ ስብሐትን የንባብ እና የሥነ ፅሁፍ ሕይወት ለመዳሰስ እና አቶ ስብሐት በስተርጅናው የልጅ ፊት እንዴት ሊኖረው እንደቻለ በሳይኮአናሊስስ ቲኦሪ መሰረት ለመተንተን የሞከሩባቸው ናቸው። እንግዲህ መጣጥፉ ስነፅሁፋዊ እና ግላዊ ሂስ፣ ኑዛዜ፣ እንዲሁም ስነልቦናዊ ትንታኔ በአንድነት የተደብለበሉበት መሆኑን ማየት ይቻላል፡፡ እኛ ደግሞ ለነገራችን እንዲመቸን ጥቢኛ ጥቢኛ እያደረግን እንፈትሻቸው፡፡
የአቶ ሚካኤል ኑዛዜ
የመጣጥፍ አቅራቢ አቶ ሚካኤል፤ ከስብሃት ገ/እግዚአብሔር ጋር በወጣትነታቸው ዘመን ስላሳለፉት ዘመን በከፍተኛ ፀፀት እና ቁጭት ይናገራሉ፡፡ በስብሐት እግር ስር ስለባከነው አፍላ ጉልበታቸው እና እድሜያቸው፣ የህልም እንጀራ ስለሆነው ተስፋቸው እና ስለተሰለበው ወኔያቸው ስብሐትን ፍፁም ተጠያቂ አድርገው ይከሱታል፡፡
ምንም እንኳን የአቶ ሚካኤል ኑዛዜ ልባችን ውስጥ ሀዘን ቢጤ ለመጫር አቅም ባያጣም ቅሉ ኑዛዜያቸው ክርክራቸውን አሳማኝ ሊያደርግ ያልቻለበት አንድ ወይም ሁለት ድካሞች እንዳለበት መጠቆም ግን ተገቢ ነው፡፡ አንዱም አቶ ሚካኤል ባከነብኝ ላሉት ወጣትነት ተጠያቂነቱን መቶ በመቶ ከራሳቸው ላይ አውርደው ስብሐት ላይ በመደፍደፍ (Blame Shifting) እንደ ግለሰብ ህይወታቸውን በተመለከተ ያለባቸውን ዋነኛ ተጠያቂነት እና ኃላፊነት በግልፅ መሸሻቸው፣ ኑዛዜያቸው አንጀት በመብላት ለማሳመን ከሚደረግ ሙከራ ብዙም ያልዘለለ አድርጐታል፡፡ አቶ ሚካኤል ይህን ያደረጉት ሆነ ብለው ይመስላል፡፡ ምክንያቱም ለህይወታቸው መበላሸት እና መኮላሸት ራሳቸው ኃላፊነቱን እና ተጠያቂነቱን በቅድሚያ ቢወስዱ የስብሐት ቀንድ እና ጅራት ይጠፋና ሰው መሆኑ ይታይ ነበር፡፡ እርሳቸው ግን ስብሐትን አንድ ግለሰብ ሳይሆን “መልአከ ሞት” ሊያደርጉት አንዴ ታጠቀው ስለተነሱ ያንን ኃላፊነት መውሰድ አልፈለጉም፡፡

ስለዚህ አስቂኝ አመክንዮ እያስተማሩን ለሂትለር መሳሳት ተጠያቂው ኒቼ ነው፣ ለኒቼ ደግሞ ሾፐንሀወር፣ ለሾፐንሀወር ደግሞ ቡድሃ… ማለት እንደምንችል ይነግሩናል፡፡ በዚህ አካሄድ ዝርዝሩ ማለቂያ ይኖረው ይሆን? አቶ ሚካኤል የሚበጃቸው ከሽሽት ይልቅ ይህ የጥፋት ምንጭ ከሰው ሁሉ ልብ እንደሚፈልቅ በማመን እና ስብሐትም እንደሳቸው ሁሉ የዚህ ምንጭ ተጋሪ እንደሆነ በማወቅ መጀመር ነው እንጂ “የስብሐት መቀነት አደናቀፈኝ” የሚለው ሰበብ ራሳቸውን በራሳቸው ለማፅናናት እና ለማሸንገል ካልሆነ በቀር፣ የስብሐትን ሥራ በአደባባይ ለማጣጣል እምብዛም የሚጠቅማቸው አይሆንም፡፡ ኑዛዜያቸውም የኤድን ገነቱን የመካሰስ ድራማ ያስታውሰናል፡፡
የአቶ ሚካኤል ኑዛዜን እንዳንቀበል የሚያሰናክለን ሌላው ምክንያት ደግሞ “ስብሐት አይኔን ገለጠልኝ፣ እርሱን ያወቅሁበት ቀን የተባረከች ትሁን” የሚሉና ከእርሱ ጋር የነበራቸውን ቆይታ እና ቁርኝት በናፍቆት የሚያወሱ ጥቂት የማይባሉ ታዋቂ ሰዎች የመኖራቸው እውነታ ነው፡፡ ይሄም እውነታ “መልክዐ-ስብሐት” ውስጥ በሰፊው ተንፀባርቋል፡፡ ግዙፍ ስም ባላቸው አያሌ ፀሐፊያን እና ገጣምያን በቀረበው “በመፅሐፍህ የምትኖር፤ ስብሐታችን ሆይ፣ ስምህ ትቀደስ” አይነት የውዳሴ ጋጋታ መካከል የስንጥር ያክል የተሰነቀረችው የአቶ ሚካኤል ኑዛዜ፤ የስብሐትን “ቅዱስ” ስም እውን ማርከስ ትችል ይሆን? መፅሐፉ አቶ ሚካኤልን በአሳ ነባሪው የተዋጠውን ነብዩ ዮናስን አስመስሏቸዋል፡፡ አቶ ሚካኤል መጣጥፋቸው እንዲካተት ባያደርጉ እና በሌላ መንገድ ቢያወጡት ይሻል ነበር፡፡ እንግዲህ አንዴ አሳ ነባሪው ውጧቸዋልና መልአኩ ሚካኤል ይርዳቸው ከማለት ውጪ ምን ይባላል?
ባህርይ እና የህይወት ዘይቤ ላይ ያነጣጠረው ትችት
አቶ ሚካኤል ምርር እርር ብለው ስብሐትን ከሚነቅፉበት ነገር አንዱና ዋነኛው ፈንጣዥነቱ እና ተድላዊነቱ (Hedonism) ነው፡፡ እኔም ራሴ የስብሐት ልቅ የህይወት ዘይቤ በመነቀፉ ቅር የምሰኝ ሰው ባልሆንም አቶ ሚካኤል ይህንን የስብሐትን ደስታ አሳሽነት እና ተድላዊነት ሲነቅፉ ቆመው የተንጠራሩበት እና ከፍታን ያገኙበት መሰረት የሆነው ቡድሂዝም (ፍልስምና (2) እና መልክዐ ስብሐትን ማየት ይቻላል) ስብሐትን ለመኮርኮም የተመኙትን ያህል ቁመታቸውን እንዳላስረዘመላቸው ልነግራቸው እፈልጋለሁ፡፡ ምክንያቱም የቡድሂዝምም ሆነ የሄዶኒዝም አስተሳሰቦች ዋንኛ አላማ እና ግብ በህልውና ውስጥ የሚገጥሙትን መከራዎች እና ስቃዮች በማምለጥ ደስተኛ እና ሰላማዊ ኑሮን መኖር በመሆኑ ነው። እነዚህ ሁለት አስተሳሰቦች የሚለያዩት ግባቸውን ለማሳካት ይበጀናል ባሉት መንገድ ብቻ ነው። የቡድሂዝም አላማ እና መንገድ ዝነኛ በሆነው እና ገራገር መስሎ አብዛኛው ሰው ሳያውቀው በሚናገረው ቅኔ ውስጥ ደምቆ ይታያል፡፡
ፅድቅና ኩነኔ ቢኖርም ባይኖርም
ከክፋት ደግነት ሳይሻል አይቀርም
የስብሐት ሄዶኒዝም ደግሞ እኔው ራሴ በፈጠርኳት ግጥም እንዲህ ተሸብልላለች፡-
ፅድቅና ኩነኔ ከሌለ ከሌለ
ስጋዬን ባስደስት ምናለ ምናለ
ታዲያ በአንድ አምላክ የፍርድ ወንበር ስር የሚበየን የፅድቅና የኩነኔን ብያኔ የሚክድ እምነት የሚያራምድ ሰው “ፈራጁ አምላክ ከሌለማ ደስ ያለኝን እንዳረግሁ ብኖር ምናለበት!!” ብሎ ለሚጠይቀው ሰው የሚሰጠው አጥጋቢ ምላሽ ከየት ይመጣል? ተድላዊነት እንደ ቡድሂዝም ያሉ ሁሉ አምላክ እምነቶች (Pantheistic) ወይም እንደ ቁስ አካላዊነት ያሉ ኢ-አማኒ አስተሳሰቦች ጭምቅ (Logical conclusion) በመሆኑ ከነዚህ አስተሳሰቦች ተነስተን ለመሞገት አቅም ያንሰናል፡፡
አቶ ሚካኤል ግን “ቡድሃ” ሳያንሳቸው የማህበረሰቡ ጠባቂ እና መንገድ ጠቋሚ ነቢይ አድርገው በሚቆጥሩት በሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ግዙፍ ቁመና ላይ በመንጠላጠል ሎሬቱ ለስብሐት እና ለብጤዎቹ በዘመኑ ያደረገውን የንሰሐ ጥሪ “ከትንቢት መፅሐፍ” ውስጥ እየጠቀሱ በከንቱ የሚሞግቱበት የባከኑ ገፆችም አሉ፡፡ ይሔም ሙከራቸው ሎሬቱ ራሳቸው በመሞታቸው ሰሞን የገቡት ሌላ “ንሰሐ” እንደነበር እንደማያውቁ፣ ካወቁ ደግሞ እንዳላወቁ ለማስመሰል እንደሞከሩ ያስነቃባቸዋል፡፡ ባለቅኔው ዛሬ በህይወት ቢኖሩ ኖሮ ለስብሐትና ለጓደኞቹ የሚያቀርቡት የንሰሐ ጥሪ አቶ ሚካኤል እንዳሉት ማህበራዊ እና አገራዊ መልክ ሳይሆን መንፈሳዊ መልክ ይኖረው እንደነበር የሚያውቅ ያውቀዋል፡፡
አቶ ሚካኤል ስብሐትን ለማንኳሰስ ብዕራቸውን አለመጠን እንዳተጉ የሚያስነቃባቸውን ፍንጭ መጣጥፋቸው ውስጥ በየቦታው ትተውልናል፡፡ ከሁሉም ባስ ያለው እና አሁንስ አበዙት የሚያሰኘው ግን ስብሐት በባህል፣ በሐይማኖት እና በልማድ ሰንሰለት ተተብትቦ ከነበረው ማህበረሰብ ጋር የነበረውን ያፈጠጠ ግጭት እና ተቃርኖ ለማድበስበስ የሞከሩበት ሙከራ ነው፡፡ በገፅ 146 ላይ እንዲህ ብለዋል “ያለ ማህበራዊና ቤተሰባዊ ኃላፊነት በዝሙት እና በአልኮል ተነክሮ ለመኖር ከነበረው የማያወላውል አቋሙ ከሚመነጭና በዚሁ ሰበብ ከሚታይ የአኗኗር እና የአስተሳሰብ ልዩነት በስተቀር ከማህበረሰቡ ጋር ምንም አይነት ማህበራዊ ተቃርኖ አልነበረውም፡፡
ስብሐት ልክ በግሪክ ትራጄዲ ውስጥ እንዳሉት ገፀ-ባህርያት በሁለት ማህበረሰባዊ ህግጋት መካከል ተወጥሮ ከገባበት አጣብቂኝ የተነሳ ራሱን መጉዳት በመምረጡ ህብረተሰቡ የሚያጨበጭብለት ትራጂክ ሄሮ ባይሆንም፣ ህይወቱ ግን ትራጂክ እንደነበር መካድ የሚቻል አይመስለኝም። ከማህበረሰቡ ጋር ያለውን ቅራኔ እና ግጭት የገለፀበት መንገድ ሳይንሳዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ሃይማኖታዊ ወይም ፍልስፍናዊ ሳይሆን ይልቁኑ ስነውበታዊ (Aesthetical) እና ህልውናዊ (Existential) መሆኑ ቅራኔ አልባ ነበር አያስብለውም፡፡ እንደውም ከአለቃ ገብረሃና በመቀጠል ከማህበረሰቡ ጋር በፈጠረው ከፍተኛ ግጭት እና ቅራኔ በጥሩም በመጥፎም ዝነኛ የሆነ ሰው ስብሃት ብቻ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡
ከዚህም በተጨማሪ በገፅ (146-147) የስብሐት የድህነት ህይወት ዘይቤ፣ ፍልስፍናዊ ማዕቀፍ የጐደለው ይልቁንስ ከስንፍና እና ራስን መግዛት ካለመቻል የመጣ እንደሆነ የሚነግሩን አቶ ሚካኤል፤ በገፅ (157) ላይ ደግሞ ድህነቱ የፍልስፍናው ውጤት እንደሆነ ይነግሩናል፡፡ ግራ በሚያጋባ ሁኔታ ዥዋዥዌ የሚጫወቱት ፀሐፊው፤ ስለ ስብሐት ስንፍና አውርተው አይጠግቡም፡፡

ነገር ግን ይሄ ክሳቸው አንባቢን እንዲያስነሳ የሚያደርጋቸው ጥያቄዎች አሉ፡፡ ስብሐትን የመሰለ የአለምን ታሪክና ስልጣኔ የለወጡ ታላላቅ መፅሐፍትን በመመርመር ዘመኑን ያሳለፈ፣ በርከት ያሉ ልብ ወለዶችን የፃፈ እንዲሁም ቁጥራቸው የማይታወቅ የጋዜጣና የመፅሔት ፅሁፎችን ይፅፍ የነበረ ሰው፣ እንዴት በስንፍና እና በዲስፕሊን ማጣት ሊታማ ይችላል? ድህነቱም ቢሆን ግዳጅ ሳይሆን ውዴታዊ (Voluntary Poverty) እንደነበረ ለማሰብ የሚያስደፍሩ አያሌ ምክንያቶች ቢኖሩም (አቶ ሚካኤል ራሳቸውን እየተጣረሱ ያቀበሉንን ጨምሮ) ለጊዜው ግን አስተማማኝ የገንዘብ ዋስትና ሊያገኝበት ይችል የነበረውን እና ስነውበታዊ ነፃነቱን ላለማጣት ሲል የሰዋውን የኩራዝ አሳታሚ ድርጅት ሥራውን ማስታወሱ ይበቃል፡፡
ስለ ስነፅሁፍ ስራዎቹ
አቶ ሚካኤል፤ የስብሐት ስነፅሁፉን አስመልክተው በሰነዘሩት ሂስ፣ አሁንም እርስ በርሱ የሚጣረስ ሃሳብ ሰንዝረዋል፡፡ አንድ ቦታ ላይ “በርግጥ በየሳምንቱ በየጋዜጦች ከሚፅፋቸው ትርጉም እና ፋይዳቸውን ለመረዳት የሚያስቸግሩ… አብዛኛዎቹ በሃሺሽና በአረቄ በነፈዘ አእምሮ ሳለ የሚፅፋቸው ፅሁፎች (ገፅ 146) ሲል፣ በሌላ ቦታ ደግሞ ስለ ስብሃት ስነፅሁፍ ስራዎች ስናወራ አንድ ልንክደው የማንችለው እውነታ ቢኖር፣ አገላለፆቹ የአንደበተ ርቱእ ጨዋታ ቁጭ ብሎ የማዳመጥ ያህል ግልፅ፣ ቀላል እና ተነባቢ መሆናቸው ነው፡፡ ይህ ችሎታው ተፈጥሮአዊ ተሰጥኦ መሆኑ እንደተጠበቀ፣ ለረጅም ዘመናት ያለማቋረጥ ከመፃፍ የዳበረ መሆኑን ማየት ይቻላል (ገፅ 177) ብለዋል፡፡ መቼም ሁለቱንም ፅሁፎች የሚያነብብ አንባቢ፣ አቶ ሚካኤል ምን እያሉ እንደሆነ ግራ ገብቶት ከመዋለል ውጪ ምንም የሚጨብጠው ነገር እንደማይኖረው ግልፅ ነው፡፡ ፀሐፊው ተቃራኒ የሆኑ ሃሳቦችን በተለያየ ቦታ ላይ ከመጠቀም ይልቅ ወገኛው መስፍን ሐብተማርያም እንደሞከሩት፤ የስብሀት ፅሁፎች የሚቀሉበትን እና የሚከብዱበትን ሁኔታና ምክንያት በአንድ ላይ አያይዘው ለማፍታታት ቢሞክሩ የተሻለ ነበር (ገፅ 226)፡፡ ይህንን ባለማድረጋቸው በሀሽሽና ባረቄ በነፈዘ አእምሮ የተፃፉ እያሉ እርሳቸው የተሳለቁበትን ዘይቤ፣ የዘርፉ ምሁራን ሱሪያሊዝም እና ፋንታሲ በሚባለው ዘይቤ ውስጥ መድበው ሲተነትኑት የሚያይ አንባቢ፣ አቶ ሚካኤልን ከመታዘብ ውጪ ምን ምርጫ ይኖረዋል?
አቶ ሚካኤል ሌላም የማይባል ነገር ይላሉ። ስብሐት ክርስቲያን ካልሆነ ኢየሱስን ለምን ያደንቃል? የቡድሀን ቃል ካላከበረ ለምን ስሙን ይጠራዋል? እያሉ ሲከሱት ጋንዲ እና ማርክስ እንኳን አይተርፋቸውም፡፡ ይህንን ሲሉ ግን “ፍልስፍና (2)” መፅሐፍ ላይ እሳቸው ከክርስትና ይልቅ ለቡዲዝም እምነት በእጅጉ የሚያደሉ ሰው ሆነው ሳለ፣ ክርስቲያናዊ ሀሳቦችን በፍቅር በተደጋጋሚ እንደተጠቀሙ ዘንግተውት ነው፡፡ እርሳቸው ለምን በስብሐት አፍ ተጠራ ሲሉ የተቆረቆሩለት ጋንዲ ራሱ፣ የሰላማዊ ትግል ዘዴውን የወሰደው እጅግ ይወደውና ያደንቀው ከነበረው ከኢየሱስ የተራራው ስብከት ነበር፡፡ ጋንዲ እራሱ ግን ክርስቲያን አልነበረም፡፡ ታዲያ ይህን እና ሌላም የሚያውቅ አንባቢ፣ ስብሐት ከጋንዲም ሆነ ከቡድሐ፣ ከማርክስም ሆነ ከኢየሱስ የተመቸውን ወስዶ ቢጠቀም ብርቅ ነው እንዴ? ብሎ ቢጠይቅ የሚገርም አይሆንም፡፡
ስለ ንባብ ህይወቱ
ፀሐፊው ባንድ ወገን በሰፊው የሚታወቀውን እና ብዙዎች የመሰከሩለትን የስብሐትን ከባድ አንባቢነት እንደሚቀበሉ እየገለፁ፣ በሌላ ወገን ደግሞ በረቀቀ መንገድ (Subtly) ስብሐት የሚባልለትን ያህል ጥልቅ እና ሰፊ አንባቢ ሳይሆን ጥራዝ ነጠቅ እንደነበር እንዲሰማን የሚያደርገንን ነገር ይነግሩናል፡፡ ስብሐት የታወቁ ፈላስፋዎችን እና ደራሲዎችን አንዳንድ አባባሎች እንደ በቀቀን ሺህ ጊዜ ለደቀመዛሙርቱ በመደጋገም ያሰለቻቸው እንደነበር ይናገራሉ፡፡ ዋንኛ ማስረጃ የሚጠሩትም ስለፍፎይድ ቲዎሪ አስተምረን ብንለው፣ ሁሌ የሚግረን “የኦዲፐስ ኮምፕሌክስን ፅንሰ ሃሳብ ብቻ” ይላሉ፡፡ ራሱን ፈፅሞ እንደ ፕሮፌሰር ማየት ከማይፈልገው እና የአስተማሪነቱን ሞያ ከተወ ዘመን ካስቆጠረው ስብሐት ታዲያ የፍሮይድን እና የኒቼን ፍልስፍናዎች ትንተና የመጠበቁ ተገቢነት ቢያጠያይቅም፤ ያነበበውን ሁሉ ከአፉ ሊያስተፉት እየወተወቱ ሰላም ይነሱት የነበሩትን አፍላ ወጣቶች፣ ባንዲት አባባል ቢገላግላቸው ጥራዝ ነጠቅነቱ የቱ ጋ እንደሆነ ማየት ያስቸግራል፡፡ የስብሀት ልዩ ክህሎት (Genius) ያለው ያነበበውን ጥልቅ ፍልስፍና አካዳሚያዊ በሆነ መንገድ በመተንተን ሳይሆን በወግ መልክ እያዋዛ እና እያለዘበ በማቅረብ ነበር፡፡ አቶ ሚካኤል አንካሳ በሆነ ማስረጃ የንባቡን ጥልቀት እና ስፋት የሚመሰክሩ በየመፅሄቱና በየጋዜጣው ላይ ያሉ በርካታ ማስረጃዎችን ትተው፣ የስብሐትን ብርቱ አንባቢነት ጥያቄ ውስጥ ለመክተት መነሳታቸው ትዝብት ላይ ይጥላቸዋል፡፡
መደምደሚያ
አቶ ሚካኤል መጣጥፋቸው መጀመሪያ አካባቢ ስለ ሲኒሲዝም (የውሻ ፍልስፍና) አውርተውልን ነበር፡፡ ፀሐፊው እዚያ ላይ አንድ ቁም ነገር የዘነጉ መስሎኛል፡፡ ውሻን ውሻ የሚያደርገው ከሰው እጅ የሚበላው ፍርፋሪ ብቻ እንደሆነ አስበዋል፡፡ እንደ እኔ እምነት ይህ ትክክል አይመስለኝም፡፡ ስብሐት ራሱ ባንድ ወቅት እንደተናገረው እና ቅዱሳት መፅሐፍት እንደሚሉት፤ ሰው ሆኖ ተቀባይ ያልሆነ ማንም የለም፡፡ ሁላችንም የምንሰጠው የተቀበልነውን ብቻ ነው፡፡ ተቀባዮች መሆን ውሾች አያደርገንም፡፡ ባይሆን ገደብ ያለን ፍጡሮች መሆናችንን ያመለክት እንደሆን እንጂ፡፡ ውሻን ውሻ ያደረገው ከሰው እጅ መቀበሉ ሳይሆን ከሰው እግር ስር ማደሩ ነው፡፡ ስብሐት ደግሞ በዚህ አይታማም፣ ቢታማም እንኳ ልቅ በሆነው ነፃነቱ እና ሽፍታነቱ እንጂ በሎሌነቱ አይደለም፡፡ እርሳቸው ግን በዚህኛውም መፅሐፍ ሆነ በ “ፍልስምና 2” ላይ እንዳየናቸው፤ ከስብሐት እግር ስር ቢያመልጡም በሌላ ሰው እግር ስር ከማደር ግን ዛሬም አላመለጡም፡፡ በቡድሃ ማለቴ ነው፡፡ ታዲያ ከዚህ የበለጠ ሲኒሲዝም ከየት ይመጣል? ዛሬም ከሰው ጉያ ሳይወጡ የስብሐትን ነፃነት እና ሽፍታነት ለመደምሰስ ምን አይነት አስተማማኝ መሰረት ይኖርዎታል?

Published in ጥበብ

(ካለፈው የቀጠለ)
(ይህን አስተያየት ለጋዜጣ በሚያመች መልኩ ለመቃኘት ሞክሬያለሁ)

ባለፈው እትም እንዳስቀመጥኩት “የተረሳ ወራሽ” የተባለው መጽሐፍ መጠንጠኛ ፍለጋ ነው፡፡ ትውልድን ፍለጋና ትምህርትን ፍለጋ መሪ መሽከርክሪት ናቸው፡፡ መለወጥ፣ መፀፀትና ይቅርታ መጠየቅ፣ መራራትና ይቅርታ ማድረግ መፍትሔ ጭብጦች ናቸው (Resolution themes)። ይኸውም ትውልዶችን ማቀራረብ፣ ስህተትን የማረምና መጪውን ትውልድ የማነጽ ዓላማ ያለው አድርጌ እንዳየው አድርጐኛል፡፡ 

ምዕራፎቹን ስንመረምራቸው፤ ደራሲዋ የኤች አይ ቪን አደጋና ከቫይረሱ ጋር የመኖር ጥንካሬን እንደማጓጓዣ (leverage) በመጠቀም፤ (እንደጠቋሚ - ታሪክ (prologue) ከምናየው የመጀመርያ ምዕራፍ ውስጥ) ከዋናዋ ገፀ ባህሪ ጋር ታስተዋውቀናለች። በኋላ ላይ በዝርዝር የህይወት ውጣ ውረዷን የምናያት ወ/ሮ ትዝታን፤ ታገናኘናለች (“ትዝታ” የሚል ስም የሰዋዊ አገላለጽ ወይም ተምሳሌታዊ ስም መሆኑን በውል አናውቅም፡፡) ከእሷ ጋር የምናገኘው ሐኪሙዋ ዶክተር ግርማ፤ ትውልድ ያወደመው፣ ሥርዓት የጐዳው ባለሙያ ሲሆን “የሥራ ተነሳሽነቱ በኑሮ ጫና እየተጨፈለቀና ርህራሄው ከሰብአዊነቱ ውስጥ እየተሸረሸረ ሲወጣ ይሰማው ነበር፡፡ ዶ/ር ግርማ ውጪ በመሄድና የግል ሥራ በመሥራት መሃል የባከነ ህይወትን የሚወክል ገፀ - ባህሪ ሲሆን ያም ሆኖ እንደ ትዝታ ጠንካራ የዘመን - ሰለባዎችን የሚታደግ፣ ተስፋ የሚሰጥ ሰው ሆኖ ነው የሚገኘው፡፡ ይህ ሰው አንዱ የዘመን ጠባሳ ነው፡፡
ኢያሱ መምህር ነው፡፡ እንደ ትዝታ ዋና ገፀ - ባህሪ ነው፡፡ እንደ ዶክተር ግርማ እሱንም ህይወት አጐሳቁሎታል፡፡ ታስሯል፡፡ መካን እስኪሆን ድረስ ተገርፏል፡፡ ተፈቷል፡፡ ኑሮ አበሳጭቶታል። የባለታሪኳ የትዝታ አሳዳጊ ነው፡፡ ከህፃንነት ለአካለ - መጠን እስክትደርስ አሳድጓታል፡፡ በኋላ ግን በድሏታል፡፡ በሁለቱ መካከል የሚፈጠረው ግጭት የታሪኩ መላ - ሰውነት ነው፡፡ በኋላ የመጽሐፉ ቁልፍ ቁልፍ ገፀ - ባህሪያት እነ አብሮ - አደጉ አወቀ፣ ዲያስፖራው የለህወሰን፣ ጓደኛው ኤፍሬም በወጉ ተሰናስለው የምናገኛቸው እያሱ በሚያደርገው የትዝታን ፍለጋ ሂደት ውስጥ ነው። ይህን መሠረታዊ ግጭት ደራሲዋ ያቀረበችው እንዲህ ነው:-
ገፅ 24 ላይ እንዲህ ታሳየናለች
የትዝታ ሃሳብ
“ትዝታ በህይወት ጥሪ በተሞላ ዕድሜዋ ላይ ስለነበረች ወደ ዩኒቨርሲቲ ስትገባ አባቷን ከብቸኝነት ጋር አጋፍጣው መሄድ ስላልፈለገች ትዳር እንዲመሠርት የምታደርግበትን መንገድ ታሰላስላለች”
የእያሱ ሃሳብ
“…ጊዜው ያመጣውን ችግር አንድ እርምጃ ቀድሞ ግብግብ ሊገጥመው በማሰብ፣ ዕውነታው የተጋረደበትን መጋረጃ ቀድዶ ከታሪኳ ጋር ሊያላትማት ወስኗል፡፡ ውሳኔውንም በተግባር አረጋገጠው፡፡ ሀቁን ከፊት ለፊት አስቀምጦ የአንቺነትሽን እውነታ እነሆ ተቀበይ አላት፡፡ “እኔኮ አባትሽ አይደለሁም፡፡
የዚህ ግጭት ውጤትም የእሱ የፍቅር/የወሲብ/ ፍላጐትና እርካታ ሆነ!! ደራሲዋ ቀጥላ እንደምትነግረንም፤
“ለዓመታት የኖሩት አባትና ልጅ በአንድ አፍታ በተከሰተ ሰይጣናዊ ድርጊት ወደተለያየና ጭራሽ ወደማይቀራረብ ተቃራኒ አለም ተሰማሩ፣ ሁለቱም በየፊናቸው ነጐዱ፡፡
የትዝታ ውሳኔ
ቀስ በቀስም ህሊናዋ መካሪ ዘካሪ፣ ቀጪና ተቆጪ ሆኖ ተጋፈጣት፤ ከዚያም እራስሺን ፈልጊ ብሎ አዘመታት (ገጽ 29) ይሄ ማንነትን ፍለጋ ነው የመጽሐፉ መሽከንተሪያ!!
ደራሲዋ፤ ዶክተር ግርማ ለትዝታ በሚመክራት ምክር በኩል የምታስተላልፍልን መልዕክት ጠንካራ የህይወት ፍልስፍና ሲሆን ትዝታ ወደፊት እምትከተለውን እንድናስብ ያደርገናል፡፡ - “…ሁኔታዎች የፈጠሩትን ችግር መጋፈጥ እንጂ መሸሽ አይጠቅምም፡፡ ሽሽት የፍርሃት ውጤት ነው፡፡ አንዴ ሽሽት ከጀመርሽ ደግሞ ሁሉም ነገር አሳዳጅሽ ይሆናል፡፡ ማብቂያ ማቆሚያ የሌለው ሽሽት፣ መጨረሺያውም ሽንፈትና ውድቀት ነው፡፡ መቼም ውድቀት አማራጭሽ ይሆናል ብዬ አላስብም፡፡”
እያሱ ትዝታን የበደለበት ሁኔታ ሰብዓዊ ድክመት (Human folly የሚሉት ዓይነት) የፈጠረው፣ እሱ አፍቅሬያታለሁ የሚልበት፣ ከፍቅር ይልቅ የወሲብ ስሜት ክጃሎት (Sexual lust or desire) የሚንርበት ሁኔታ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ ድርጊቱ ተዓማኒና ጥንካሬ እንዲኖረው አመክንዮው/ያነሳሳው ሁኔታ፤ ብርቱ ትንታኔ ቢሰጥበት መልካም ነበር፡፡ ቀስ በቀስ ያደገ ስሜት መሆኑን የሚያጠይቅ (justification የሚሰጥ) ማሠሪያ አንቀጽ ቢኖረው የገፀ - ባህሪውን ድርጊት እንድንዘጋጅበት ያደርገን ነበር፡፡ በተለይም በሁለኛው ምዕራፍ በወጉ የምናገኛት ዋናዋ ገፀ ባህሪ ትዝታ ግን ከእያሱ መለያ ሰበቧ ተዓማኒ ነው፡፡ ወደፊት የሚጠብቃትን ህይወት ለመጋፈጥ ቆርጣ ስትወጣ የምናይባት ወኔም ገፀ - ባህሪዋን በቅጡ የሚሸከም ነው፡፡ ለመማር ያላት ፍላጐት፣ ወላጅ አልባነትን መቋቋም፣ የማንነት ፍለጋን መጋተር፣ ማህበራዊ ኑሮን ማሸነፍ፣ ሥራ ፍለጋ፣ የኢኮኖሚ ችግር፣ ልጆች ማሳደግና ማስተማር…ከሁሉም በላይ ፍላጐቷን የማይረዳላት ማህበረሰብ ውስጥ መኖር (misunderstood እንዲሉ)፤ ለገፀ - ባህሪዋ በጠንካራ ድርና ማግ መሠራት ምስክር ነው፡፡
ሌሎች ገፀ ባህሪያት
ኤፍሬም የእያሱ ጓደኛ በዘመን - የታሰረ (ወይም ባሁኑ ዘመን አነጋገር “የተቸከለ” stuck in time) ገፀ ባህሪ ነው፡፡ ሚናው እየጐላ የሚሄደው ወደኋላ ላይ በመሆኑ ገፀ - ባህሪውን ገና ስናውቀው ፋይዳው ግራ ያጋባል፡፡ ዋለልኝ ከውጪ የመጣና የሸሸውን ማህበረሰብ ሊክስ የመጣ ዳያስፖሬ ነው፡፡
የእያሱ ሠራተኛ ብርቄ በቅጡ የተሳለች የቤት ሠራተኛ ባህሪ ናት፡፡ ሆኖም የወሰደችው ቦታ የበዛ ይመስለኛል፡፡ አጠር አድርጐ ፋይዳዋን ማሳየት ይቻል ነበር፡፡
አንድ እጅግ የማረከኝ ሃሳብ፤ እያሱ ወደ ወላጆቹ ቤት ጂጂጋ ሄዶ ከታሰሩት ጓዶቹ እነማ እንደሞቱና እነማን እንደተረፉ ለመመዝገብ መነሳቱ ነው፡፡ ታሪክን ለመፃፍ ትውልድን ለማስታወስ፣ደራሲዋ ያላትን ፍላጐት ለማርካት የጣረችበት ዘዴ ወይም መላ - ይመስለኛል፡፡ ደስ ብሎኛል፡፡
መጽሐፉ በእናትና ልጅ የተሞላ ነው፡፡ ልዩም፣ ማህበረሰብ -ተኮርም፤ የሚያደርገው ያ ነው፡፡ በማንኛውም ህብረተሰብ የችግር ገፈት ቀማሾች እናትና ልጅ ናቸው እንደማለት ነው መጽሐፉ ያሰመረባቸው! ባለታሪኳ ትዝታ የሁለት ልጆች እናት ናት፡፡ የቤት ሠራተኛዋ ብርቄ ባለልጅ ናት፡፡ የትዝታ እናት አራሷን ትዝታን ይዛ የመጣች ናት፡፡ ትዝታ ደሴ የኖረችባት እናት ልጆች አሏት፡፡ የዐወቀ ሚስት ባለልጅ ናት፡፡
የሺመቤት፣ ትልቁ ልጇ የተገደለና ከትንሽ ልጇ ጋር የምትኖር ነበረች…እናትና ልጅ!
እንግዲህ መጽሐፉን በውርድ ስናየው፡፡ የአንዲት ወላጅ አልባ ሴት ህይወት፣ በኤችአይቪ መያዝና በወጉ ከቫይረሱ ጋር ለመኖር መቻል፣ እያሱ የተባለው መምህር ዋናዋን ባለታሪክ ትዝታን በአደራ ማሳደግ (እናት ወ/ሮ መውደድ ቤቱ ድረስ መጥታ ያስረከበችው መሆኑ፤) አደራውን ለማሳካት ለወላጆቹ መስጠቱ፣ ባለታሪኳ አድጋ ወደሱ መምጣቷ፤ ለአካለ መጠን ስትደርስ ስለተኛትና ስለደፈራት ቤቱን ጥላ መጥፋቷ፣ የአሳዳጊዋ እያሱ መታሰር፣ የወጣቶች እጅ መስጠት፣ የእያሱ ከእስርና ከሞት የተረፉ ወጣቶችን መመዝገብ፣ በፋሲካ ዋዜማ የብዙ ወጣቶች መረሸን፣ ሰፊ መቼት ፈጥረው፤ እያሱና አዲሱ ትዳሩ፣ የእያሱ አወቀን ከልጁ ማገናኘት ድረስ ተጉዞ፣ የማራዘሚያ መድሃኒት መውሰድ የጀመረችውንና የኤች አይ ቪ ጉዳይ አስተማሪ የሆነችውን ትዝታን እስክናገኝ የሚዘልቀውንና የዳያስፖሬው የዋለልኝ የሞቱ ባለታሪኮችን ፍለጋ መምጣት፣ የእያሱ፣ የኤፍሬምና የየለህወሰን የተወሳሰበ ግንኙነት ተንተርሶ የየለህወሰን ማንነት መገለጥ፣ የትዝታ ወንድም ልጅ መገኘት፡፡ የታሪክ ፍሰቱን እንዲፈታተነን በሚሞክር መንገድ የሚወርድ ነው የትዝታ የነኤፍሬምና የአክስቶቿ ግንኙነትና የቤተሰብ ድርጅት በ3ኛው ሚሌኒየም ማቋቋም፤ ማክተሚያው ነው፡፡
ካለፈው የሥርዓት አውዳሚ እርምጃ በኋላ በተፈጠረው ሁኔታ ላይ የተመሰረተው የመጽሐፉ የግራና ቀኝ የፍትጊያ አቅጣጫዎች (war zones):- ወገን አልባነት፣ የማንነት እጦት፣ ሥር - አልባ መሆን፣ መገለል፣ መገፋት፣ መቀጨት፣ ሥራ - አጥነት፣ የትምህርት እጦት፣ የኢኮኖሚ ችግር ባንድ ወገን፡፡
በሌላ ወገን መለወጥ፣ ቁርጠኝነት፣ በራስ መቋቋም፣ ራስን - መቻል፣ ፀፀትንና መከፋትን መጽሐፍ በመፃፍ መወጣት፣ ጽንዓትና ትዕግስትን የያዘ ነው፡፡ እንደዋና የመጽሐፉ ውጤት ልናገኘው የምንችለው ቁም ነገር:- ስህተትን ተረድቶ ይቅርታ መጠየቅ፣ ይቅርታ ማድረግና ለቀጣይ ህይወት ተዘጋጅቶ መንገድ መቀየስ ነው፡፡
በመጽሐፉ መሀል መሀል የምናገኛቸውን ቁምነገሮች በንዑስ ርዕሶች አንዳንዶቹን ልነቁጥ :-
በወቅቱ ት/ቤት - የተማሪና መምህራን ግንኙነት
“ተማሪዎቹና መምህራኑ የመሰረቱት የጠበቀ ግንኙነት ወደኋላ በአገሪቱ ውስጥ ለተስተጋባው የትግል ጥሪ የጋራ ምላሽ እንዲሰጡ አድርጓቸዋል…ህይወት በራሱ ስጋት ሆነ - ከተሞች የሰላም መንፈስ ራቃቸው፡፡ በከተማው የተከሰተው ሁኔታም የእያሱንና የሌሎች መምህራንን የትግል ተሳትፎ በእጥፍ አጐለበተው፡፡ የትግል ሥልታቸውንም ለወጠው፡፡ በየዕለቱ የሚጐርፉትን ወጣት ተሰዳጆች በማስጠለልና ከአደጋ ጠብቆ በማቆየት ተግባር ተጠመዱ፡፡ አስተማማኝ መሸሸጊያ ወደሆነው የገበሬ መንደር ወጣቶችን ማሸጋገር የመምህራኑ የዘወትር ሥራ ሆነ፡፡” የእያሱ ገፀ - ባህሪ የተሳለው በዚህ ሚሥጥራዊ ክንዋኔ ውስጥ ነው እንግዲህ፡፡
የትውልዱ የጋራ ስሜት በሚከተሉት መስመሮች ይታያል
እያሱ ቤት፤ በእንግድነት የመጣችውን መውደድን ስለታቀፈችው ልጅ የሚጠይቅበት ሁኔታ፡-
“ልጅሽ ወንድ ነው ወይስ ሴት?”
“ሴት ናት” ህፃኗን በስስት ጐንበስ ብላ እያየች መለሰችለት፡፡
“የማናት? ማለቴ አባቷ ማን ነው?”
“የሁላችንም ናት፡፡ የእኔ፤ የአንተ፣ የትግሉ የዘመኑ ልጅ ናት” አለችው ፍርጥም ብላ፡፡
የትውልዱን የጋርዮሽ ስሜት ብቻ ሳይሆን መጽሐፉ የልጅቷን ማንነት ሚሥጥራዊ በማድረግ ቀጣይነቱን ያረጋግጥልናል፡፡ ፍለጋ እንድንቀጥልም ይገፋፋናል፡፡
ትዝታን የአባቷ መክዳት ጐድቷታል
ትዝታ እያለቀሰችና ውስጧ በቁጭት እየተቃጠለ፣ለትዳሯና ለልጆቿ ስትል የከፈለችውን መስዋዕትነት፣በባሏና በዘመድ አዝማዶቹ የደረሰባትን ግፍ በዝርዝር አስረዳችው (ገጽ 472)
ከመጽሐፉ ያገኘሁት ትምህርት
የእያሱ መረጃ የማሰባሰብ ሙከራ ለእኛ ትውልድ መልዕክት የሚያስተላልፍ ነው ብዬ ገምቼዋለሁ፡፡ ትውልዳችን የት ደረሰ፣ ምን ደረሰበት? ምን ተማርንበት? ለማለት ያለና የሞተውን፣ የጠፋውንና የተሰደደውን፤ መመዝገብ ለብዙ ታሪካዊ እሴት አስተዋጽኦ ያደርግ ይመስለኛል፡፡
ዘናና ላላ የሚያደርጉ ትዕይንቶች አለመኖር
ጽሑፉ ባለፈው እንዳልኩት የምሬትና የሐዘን ምርቅ የበዛበት በመሆኑ ዘናና ላላ የሚያደርጉ ትዕይንቶች (relief scenes) ያስፈልጉታል፡፡ የዚህ ዓይነት ትዕይንት አንድ ቦታ ብቻ ነው ያየሁት - ገጽ 459 ላይ የምናገኘው፡፡
እንደዋዛ ማዳበሪያ ሆኖ የገባው ዝናቡ ጭሮ ወይም ዝናቡ በርጮሌ ነው፡፡ ለአብነት እንየው:-
“ታዲያ ወደፊት እንዴት ላገኝህ እችላለሁ?” አለው የለህወሰን ከቦርሳው አውጥቶ አስር ብር እየሰጠው፡፡
“ግዴለህም አታጣኝም፤ ዝናቡ ጭሮ ወይም ዝናቡ በርጮሌ ብለህ ብትጠይቅ ማንም ያሳይሃል፤ ገንዘብ እንጂ ሰውና ችግር ፈልገው አጥተውኝ አያውቁም… ይልቅ መኪናው ላይ ላሳፍርህ” አለው፤ 10 ብሩን ግንባሩን አስነክቶ ወደ ደረት ኪሱ እያስገባ፡፡ የለህወሰን በልጁ አነጋገር አዝኖ ሌላ 10 ብር ጨመረለት፡፡ ልጁ በደስታ ዘለለ! አቀፈው፤ ሳመው፡፡ ካሣፈረው በኋላ የለህወሰን የሰው ብዛት ሲያንስበት ተበሳጨ፡፡ ዝናቡ ግን “አንተ ማሰብ ያለብህ ስለሰዓቱ ነው…አምስት ሰዓት እየሆነ አይደል…በዚህ ሰዓት የማይሆን ነገር የለም፡፡ ሾፌሩ ከነሸጠው ያላችሁትን ተሳፋሪዎች እንደ አምሳ ሰው በመቁጠር ተነስቶ እብስ ለማለት ይችላል” ይለዋል፡፡
መምህር አበጀ እና ትዝታ
አበጀ የትዝታ ባለውለታ - ብቸኛ ሠናይ ባህሪ ነው፡፡ ደሴ ወስዶ ት/ቤት ያስገባት እሱ ነው፡፡
እሱም ግን እንደ ዶ/ር ግርማና እንደ እያሱ በሚሰራው ሥራ ደስተኛ አልነበረም፡፡ (የሰራተኛው የሥራ ተነሳሽነት ማጣት አንዱ አንኳር ጉዳይ መሆኑን እዚህም እናያለን) ውጪ ድርጅት ሲቀጠር ቤተሰቡን ይዞ ወደ ወሎ ሄደ፡፡ ትዝታን ወደ ደሴ ይዟት የሄደው ለዚህ ነው፡፡ ይህም ነው የትዝታን ደብዛ ከእነ እያሱ የጠፋባቸው፡፡
የሀገራችን ማስታወቂያዎች
ደራሲዋ፤ ስለሀገራችን ማስታወቂያ ባህል እግረ መንገዷን ልታሳየን ሞክራለች፡፡ በገጽ 450 እንዲህ ትላለች - በየለህወሰን አስተሳሰብ ውስጥ ሆና “በቲቪ ማስታወቂያ ሁሉም ከማሳየት ይልቅ በመናገር ላይ የተመሰረቱ መሆናቸው ነው፡፡ ለዚህ ሁለት መነሻዎችን አሰበ
1) ምናልባት ምንጫቸው የቴአትር ጥበብ መሆኑና በወጣትነታቸው
በድራማ የኖሩ መሆናቸው
2) በልምድም በትምህርትም ከትያትር ጥበብ ጋራ ራሳቸውን ያጣበቁ ግለሰቦች ከድራማ ውጪ መልዕክት ማስተላለፊያ የሌለ ስለሚመስላቸው
(3ኛው)ና ዋንኛው፤ የህብረተሰቡ አንድ መልዕክት ከማየት ከሁለት ሦስት ሰው ለመስማት የመምረጡ ባህል ነው!
መጽሐፉ እንደመጀመርያ መጽሐፍ፣ እንደማሟሻ፣ ግዴታውን ተወጥቷል፡፡
እንደምክር
የገጽ ብዛት ለሚያስደነግጠው የዛሬ አንባቢ፣ ከዋናው ጉዳይ የራቁ በጣም የተዘረዘሩና የተደጋገሙ አንቀፆችን በማውጣት ብንተባበረው ደግ ነው፡፡ ማቀላጠፍ ማለት ነው፡፡
የገፀ - ባህርያት መብዛት የመጽሐፉን ሰንሰለት እንደሚያስረዝመው፣ አልፎ አልፎም ሊያደናግረው እንደሚችል ማስተዋል፡፡

Published in ጥበብ

           የክረምቱ ዶፍ ውስጥ ሆነን ሙሽራ ጀንበር የምንናፍቀው በተስፋ ነው፡፡ የብርሃን ቬሎ አጥልቃ ብቅ የምትለው የመስከረም ሰማይ ጀንበር - ከአደይ አበባ ጋር እየጠቃቀሰች መሣቅዋን የምናነብበው ዛሬ ለምቦጩን ከጣለው ሰማይ ሥር ተኮራምተን ነው። ግጥሞችም እንደ አበባ ናቸው፤ በተስፋ ይስቃሉ፣ በትካዜ ይጠወልጋሉ፡፡
ዛሬ የሰው ልጆች የገደል ማሚቱዎች ናቸውና በአብዛኛው እንደኛው ቀይ፣ ጥቁር፣ ጠይም ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ በቅርፃቸው ሳይሆን በይዘታቸው፡፡ እንደኛው ደም አላቸው፤ ይሞቃሉ፤ ይቀዘቅዛሉ። እንደኛው ልብ አላቸው፤ ይዘለልላሉ፤ ሕይወት ይረጫሉ፡፡ ምናልባትም በዚህ ዝምድና እንነፋፈቃለን፡፡ ሰው ከሌለ ግጥም የለም፤ ሰውም ያለ ግጥም ዝም ብሎ የተገተረ ጭራሮ ነው፡፡ በዜማ ያለቅሳል፣ በዜማ ይደንሳል፤ በዜማ ይተክዛል፣ በዜማ ይጽናናል፡፡ ይፈነጫልም! ሰውና ግጥም፣ ግንድና ሀረግ ናቸው ልበል? ማነው ሀረጉ? ቀን ይመልሰው፣ ብለን መዝለል አንችልም?...የጥያቄውን አጥር?...ሰውም ግጥምም ጥያቄ ነው፤ በጥያቄ የተጠቀጠቀ። በሃሳብ የሚነድድ እሳት! ታዲያ ሁለቱንም ችቦ አድርገን በአንድ ደመራ ስር ከምረን ሲነድዱ ይኑሩ ብለን እንተዋ!...አዎ!
አሁን የወጣቷ ገጣሚ ጽጌ ተምትም ግጥሞች መሠሉኝ ስሜቴን የቆሰቆሱት፣ የነካካቻቸው ነገሮች ደም አላቸው፤ ነፍስና ትንፋሻቸው፣ መዐዛና ዜማቸው ወደ ውስጥ ይዘልቃል!
ገጣሚዋ እኔ መግቢያዬ ላይ ስለተናገርኩት የአዲስ ዘመን መባቻ የምትለው ነገር መጀመሪያ ቀልቤን ሳበው፡፡ መጽሐፉን እንዳገኘሁ ማረፊያ ቦታ እስካገኝ ድረስ ያላቆዩኝ ግጥሞች ነበሩና አለፍ አለፍ እያልኩ ማየት ግድ ሆነብኝ፡፡ የጀርባው ግጥም ነው የልቤን ልብ ያንጠለጠለው፡፡
“መሬት ጥል ነጥፎባት፤
ጅብ በበቃው ሥጋ፤ ውሾች ሲራኮቱ ድምጽ ከተሰማ፣
ሊነጋ ነው ሌቱ ጐህ እየቀደደ፣ ሰማይ እየደማ፡፡” ይላል ግጥሟ፡፡
ጅብ እስኪበቃው ሲበላ፣ ጅብ ጠግቦ ሲተርፈው፣ ምን ያህል ጥንብ እንዳለ መገመት አያዳግትም፡፡ ማነው ግን ሟቹ? ብቻ እንዲህም ሆኖ በዚህ ሞት በገነነበት ፍርሀት ጉሮሮ ላይ ትንፋሽ ባሳጠረበት፣ ፀሊም ድባብ ውስጥ አሁንም ተስፋ አለ ትላለች። የሰው ልጅ ሕይወት ግዝፈቱ ምናልባት የተስፋ አቅሙ ሳይሆን አይቀርም ወደሚለው ድምዳሜ ትገፋናለች፡፡ ግን ደግሞ ጐህ ሲቀድ በነፃ አይደለም። ሰማዩ ስለ ብርሃን ደምቷል፡፡ ስለ ብርሃን ዋጋ ከፍሎዋል፡፡
ጨለማው የሚነጋው፣ እንቆቅልሹ የሚፈታው በዚህ ዋጋ በከፈለ ብርሃን ነው!
“ይነጋል?” ብላ ትተነብያለች ጽጌ!
ገጣሚ ጽጌ አሁንም “ትንቢት” በሚለው ግጥምዋ ታፏጭልናለች፡፡
ኑ…“ቃ” ቃ - እንጫወት
የቅጠል እንጀራ የጭቃ ዳቦ እንጋግር
ጠላ እንጥመቅ ከሳር፣ ቡና እናፍላ ከአፈር
ኑ…ቃ ቃ እንጫወት
ቆርኪ አለ ለስኒ፤ ጆግ አለ ለጋኑ
ኑ፡፡
ደረሰና ዛሬ - የልጅነት ትንቢት
ቢቸግረኝ የውነት ቁራሽ ባትኖር በቤት
የውሸት፣ የውሸት፡፡
ኑ… “ቃ” “ቃ” ንጫወት፡፡
የብዙዎቻችን የልጅነት ትዝታ ፊታችን ድቅን የሚያደርገው ይመስለኛል፡፡ ጓደኞቻችን ይታሰቡናል፡፡ “ቡና ጠጡ” ተባብለን ከቆርኪ ከንፈር ጋር እየተሳሳምን አየር የሳብነው - ይታሰብናል፡፡ ደሞ እዚያው አንቀርም፤ ወዳነፀረችበት ሕይወት መጥተን በርካታ በሮችን እናንኳኳለን፡፡ መጨረሻችንም ከንፈር መምጠጥ ይሆናል፡፡
ጽጌ ልጅነትን ከነምናምኑ ፊታችን ደርድራዋለች። ደርድራ አልተወችም፤ ለዛሬ ሕይወታችን መልክ ማያ መስታወት አድርጋ አስቀምጣለች፡፡ ቅሬታ አላት፤ ለምን የሚል ጥያቄ ግጥሞችዋ ውስጥ ተገትረዋል፡፡ ለምን እንደ ልጅነታችን ጨዋታ የእውን ሕይወታችን ባዶ ሆነ? ለምን ጓዳችን አልሞላ አለ? ብላ አግድም እያወራች ነው - በዜማ!...አብረን እናጐራጉር ነው ነገሩ! መጀመሪያም ግጥም እየነደደ - ያነድዳል - ብዬ የለ! ..አንድ ደመራ ውስጥ ልንጣድ ነው፡፡
“ዝምድና 2” በሚል ርዕስ የተፃፈችው መንቶ ግጥም - ስለጊዜና ስለለውጥ ግዙፍ ሃሳብ የተሸከመች ይመስላል፡፡ እንዲህ ትላለች፡፡
እንኳንስ ለመንካት፣ ለእይታ ር….ቆ የተሰቀለ ሥጋ
ቋንጣ ሆኖ ይወድቃል - ቀን እየመሸ ሲነጋ፡፡
ይህች ግጥም ዜማ ትሠብራለች፡፡ ግጥሟ ምናልባት ሥጋዊ ውበትንም የምትወክል ይመሥላል። ጊዜ የሰውን ውበት ዘልዝሎ ቋንጣ ያደርገዋል፡፡ ከዚያም ይወድቃል፡፡ ብቻ የገጣሚዋ አይኖች ጠለቅ ያሉ ናቸው፡፡
“የሞት ስዕል 1” የሚለውን ግጥምዋን ደግሞ እንየው :-
“የእጆቼን አሻራ፤ የመዳፌን መስመር
ቀለሙን ጉዞውን “ባይኖቹ ቆምሮ
“ሞትሽ” ቀርቧል ያለኝ ቀኔን አሳጥሮ
ጥንቆላው ሰምሮለት - ሞቴን “ባይኔ አየሁት
እፀዳን አሳልፌ በ እንደሰጠሁት፡፡
ግጥሙ የመዳፍ ንባብን የቀጣዩን ዘመን ትንበያ በቀጥታ ቢያሳይም፣ በገፀ ባህሪዋ አንፃር ሲታይ አንደኛው ተባዕት ገፀ ባህሪ መዳፍዋን አይቶ፣ ሞትዋን ያሟረተባት ነገር እውን መሆኑ ያንገበገባት ይመስላል፡፡ ሞትዋ ደግሞ አፈር ገብቶ እስትንፋስን ዘግቶ መሰናበት ሳይሆን፣ በቁም ሳሉ መሞት ነው። የግጥሙ ተራኪ እንስት፣ ሞት በፍቅር እጅዋን እያሻሸ ያሟረተባት ተባዕት እጅ መውደቅዋ ነው። ግጥም ከዚህ በላይ ተርትሮ ገመናውን ባያሳይ ግድ አይባልምና “ከእጅ ያውጣት” ብሎ ደግ ደጉን መመኘት ነው፡፡
የጽጌ “ፀፀት” የተሰኘ ግጥም እስካሁን ስለፀፀት ካነበብኩዋቸው ግጥሞች በተለየና በሚገርም ሁኔታ የተገለፀ ነው፡፡
“በሞኝነት ብልጠት ስቶ፤ ሳያስቡት እንደቅዠት
የያዙትን ድንገት ሲያጡ
ብዙ ናቸው ቅጠሎቹ፤ ከሀዘን ልብ ተሸምጥጠው
በዓይኖች ላይ የሚረግፉ - በጉንጮች ላይ የሚሰጡ፤
የእምባ ግንድ ልብ ውስጥ ነው፤ ቅርንጫፉም ከዚያው ይመዘዛል፤ ቅጠሎቹ - የእምባ ዘለላዎች በሀዘን ተሸምጥጠው ጉንጭ ላይ ይሰጣሉ” ትላለች ግሩም ምሰላ፣ ግዙፍ ምናብ ነው፡፡
ግጥሞችዋ ብዙዎቹ ስሜት…የሚያስደምጡ ሌሪኮች ሆነው ለዛ ባላቸው ቃላት፣ በጥሩ ስነ ግጥማዊ አሰኛኘት ደርድራቸዋለች፡፡ አጫጭር ሆነው ዘለግ ያለ ታሪክና ሁነት የያዙ፣ ረዝመው የቃላት ትንፋሽ የማያጥራቸው ግጥሞች አሏት፡፡
ለምሳሌ ይህቺ አራቶ - ግጥም ታስደምማለች
ነፍሱ ስንፍናን ለለመደ
ኑሮውን ለቀኑ ለሚያማ
ህይወትን አትንገሩት
አያዳምጥም እየሰማ
በዚህች ግጥም - “ነፍስ” ውስጣዊ ማንነትን የምትወክል ናት፡፡ ስሜት፣ ዕውቀትና አእምሮ በእርሷ ይጠቀለላል የሚለው እምነትም የዘገየ ነው፡፡ ታዲያ ገጣሚዋ ስንፍና ኑሮዋ ስለሆነች ነፍስ ባለቤት በተባዕት ፆታ ታወራለች፡፡ ስንፍና እንደ ድንጋይ ተከምሮበት ሰበብ እየመዘዘ በየቀኑ ለቀን ጆሮ ኑሮውን ለሚያብጠለጥል ሰው፣ የሕይወትን ትርጓሜ በመተንተን፣ የውበትን ሥዕል ለማሳየት፣ አትድከም ብላ ሦስተኛ ሰው ትመክራለች፡፡ እያንዳንዱ አንባቢ ሦስተኛ ሰው ነው፡፡ ይተረክለታል፡፡ ምናልባት ደግሞ ሁለት ቦታ የሚገኝ ሰው ሊሆን ይችላል። ወይም እንችላለን፡፡ ሰነፍ ከሆንን በስንፍናችን ከምንቀምሳት ልምጭ ሌላ፣ እንደገና ሌላ የምክር ቃል ይጠብቀናል፡፡ “አትድከም ሰነፍ ይሰማል እንጂ አያዳምጥም፡፡ ለዚህ የሚሆን ቀልብ የለውም፤ ጊዜውን አባክኖ ያንተን ጊዜ እንዳያባክን ተጠንቀቅ…ነው ነገሩ፡፡
“ማነው ባለጋሪ?”ን ሳነብብ ሁለት የስነግጥም ምሁራን ትዝ አሉኝ፡፡ ኤስ ኤች በርተን፣ ለውረንስ ፔሪኒ “ስነግጥም በቀላል ቋንቋ ጠሊቅ ሃሳብ ሊይዝ ይችላል፤ ቃላት ብቻ ግጥም አይሰሩም” የሚል ሃሳብ አላቸው፡፡ እንዲህ ትለናለች ገጣሚዋ ጽጌ :-
ላቡን አንጠፍጥፎ ሀገር እየዞረ
በእጅ እግሩ እየደቃ - ጋራ እየሾፈረ
ለሱ ባይከፈል፤ ባይደርሰው ስባሪ
ሰው ወይስ ፈረሱ …ማነው ባለጋሪ?””
ገጣሚ የሚደነቀው ይሄኔ ነው፡፡ ያነሣችው የፍትህ ጥያቄ ነው፡፡ ለመሆኑ ሰውን ባለጋሪ ያደረገው ማነው? ጋሪውን እርሱ አይጐትት፣ ብረትና እንጨቱን እርሱ አልተሸከመ! … ግን በብሩ ስለ ገዛ “አያ እገሌ … ባለጋሪው” ይባላል፡፡ ልብ ያላልነውን ልብ ብላለች፡፡ ነገሮችን ባልታዩበት መንገድ ማየት የገጣሚ አንዱ ብርቅ ተሰጥዖ ነው፡፡
“የዝንቦች ጨዋታ” ሌላኛው “የሽልንጓ ሴት” ግጥም ነው፡፡
በመሶብሽ ሞልተው ከእንጀራሽ ከወጡ
በእጃቸው በእግራቸው ባ’ፋቸው እያወጡ
ሲያሻቸው ሲበሉ፣ ሲያሻቸው ሲረግጡ
ጥጋባቸው በዝቶ ሌማትሽን አርክሰው በቆሻሻ ጩኸት
ወዲያ ወዲህ ሲሉ በመሶብሽ አናት
አይኖቼን አንስቼ የበለሉትን ባየው!?
እናት ሙች! ሙሽ!
ያው እንዳስቀመጥሽው አንዳ=U ሳይነካ፤
የዝንቦች ጨዋታ እንደዚህ ነው ለካ!
“የሽንልጓ ሴት” ውስጥ ጥቂት የማይባሉ ግጥሞች ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆኑ ባለ ሁለት መልክ መልዕክት የያዙ ይመሥላሉ፡፡ አሊጐሪ ሰምና ወርቅ ናቸው፡፡ እማሬያዊና ፍካሬያዊ እንደምንላቸው ዓይነት መልዕክቶች በውስጠ ወይራነት ሙሉ መልዕክት ያስተላልፋሉ፡፡ ይሁን እንጂ ግጥም መልዕክት ማስተላለፍ ዋና ዓላማው አይደለም፡፡ በሚያስደንቅ መንገድ መኮርኮር ግን የላቀ ችሎታ ይጠይቃል ባይ ነኝ፡፡ ወጣት ገጣሚያን እንዲህ ሠርሠር አድርገው፣ አድማስ ዘልቀው ካዩ፣ ነገ ደግሞ ሌላ ውበትና ሌላ ልዕቀት ይመጣሉ፡፡ ሌላው እጅግ አይረሴ ነገር ግጥም የሙዚቃ ብልት መሆኑ ነው፡፡ ሙዚቃ ዓለም አቀፍ ቋንቋ ነውና፣ በፈረሳይ በእንግሊዝ፣ በላቲን፣ በግሪክ ቢሆን ያለ ቃላት ትርጓሜ እንኳን ልባችንን ሊያስመታ፣ ስሜት በደማችን ጫንቃ ሊጋልብ ይችላል፡፡ ላምቦርን እንዲህ እንደሚሉት፤ “most fatal mistake we can make regard to poetry is to forget that poetry was born of music and is a form of music” ገጣሚት ጽጌ ተምትም በዜማ ግጥም ሸጋ ጅማሬ አላት፡፡ የነገዋ ብሩህ ሣቅም ደማቅ ሆኖ እንደሚመጣ ተስፋ አለኝ፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 03 August 2013 10:51

ያልነገርኩሽ ነገር

(ካለፈው የቀጠለ)
ሀሌሉያ ሚናን እንዳፈቀረው አፍቅሮ አያውቅም፤ ኧረ እሱ ጭራሽ አፍቅሮ አያውቅም፤ አሁን ግን የሚያስበው ስለ ፍቅር፣ የሚያነበው ስለ ፍቅር፣ የሚያደምጠው የፍቅር ሙዚቃ ነው፡፡ በየቀኑ ከሚሰማቸው የፍቅር ዘፈኖች የወደዳቸውን ሀረጎች ስንኞች እየፃፈ ለሚና ስልኳ ላይ ይልክላታል። የትኛውም ሀረግ፣ የትኛውም ስንኝ ግን እንደልቡ አልሆነለትም፣ ግን ዝም ከማለት ይሻላሉ ብሏል፡፡
ከሚልክላት እያንዳንዱ መልእክት ሥር እንዲህ የሚል ሀረግ ያክልበታል፡፡ “ግን ያልነገርኩሽ ነገር አለ፡፡”
“ከወደድኩሽ በላይ ወደድኩሽ መልሼ …”
(ግን አንድ ያልነገርኩሽ ነገር አለ)
“Truly, Deeply, Madly …”
(ግን አንድ ያልነገርኩሽ ነገር አለ)
መውደዴን ወድጄዋለሁ …”
(ግን አንድ ያልነገርኩሽ ነገር አለ)
“I love you eight days a week …”
(ግን አንድ ያልነገርኩሽ ነገር አለ…)
Said I love you but I lied, cause this is more than love I feel inside.
(ግን አንድ ያልነገርኩሽ ነገር አለ)
(ሀሌሉያ ከላይ የተጠቀሱትን ሀረጎች የወሰዳቸው፣ በቅደም ተከተል፡- ከጥላሁን ገሰሰ፣ ከሳቬጅ ጋርደን፣ ከዳዊት መለሰ፣ ከዘ ቢትልስ፣ ከቴዎድሮስ ካሳሁን፣ ከማይክል ቦልተን የፍቅር ዘፈኖች ነው፡- ደራሲው፡፡)
ግን አንድ ያልነገርኩሽ ነገር አለ የሚለው ያልነገራት ነገር ኖሮ አይደለም፤ ሁሉን ነገር ነግሯታል፤ ግን ቢነግራት፣ ቢነግራት፣ አልጠግብ ያለው … እንደሚወዳት ነው፤ እና አንድም ቀን እንደሚወዳት ነግሯት የሚያውቅ አይመስለውም። ደውላ ወይ አግኝታው፡- “ምንድነው ያልነገርከኝ ነገር?” ብትለው “እንደምወድሽ ነዋ!” ይላታል፡፡
ኧረ እንደውም ጠይቃዋለች፡-
“ምንድነው ያልነገርከኝ ነገር?!” አለችው አንድ ቀን ቆጣ ብላ፡፡
“እንደምወድሽ ነግሬሽ አውቃለሁ እንዴ?” አለ የምሩን፡፡
“አስጠሊታ፤ ያልነገርከኝ ነገር ምንድነው?”
“ምንም ያልነገርኩሽ ነገር የለም፤ የደበቅኩሽ ምስጢር እንደምወድሽ ብቻ ነው፡፡”
አንድ ቀን፡-
“ከአሁን በኋላ የማንንም ሙዚቃ፣ የማንንም ግጥም እንድትጋብዘኝ አልፈልግም፣ ከአሁን በኋላ የምፈልገው የአንተ ቅንብር የሆነ ሙዚቃ፣ የአንተ ድርሰት የሆነ ግጥም፣ የአንተ ቅብ የሆነ የሥዕል ሥራ ነው፡፡”
“እሺ እስማማለሁ፤ ግን ለመጨረሻ ጊዜ የገብረክርስቶስን፣ አንድ ግጥም ልበልልሽ፡፡” እስከዛሬ የራሱን ገለፃ ተጠቅሞ ፍቅሩን ባለመግለፁ፣ እሷም ይህን አስተውላ በግልፅ በመናገሯ አፈረ፡፡
“ከዚህ በኋላ ያንተ ካልሆነ የሌላ የማንንም አልፈልግም፡፡”
“መልካም”
የሚወደውን የገብረክርስቶስ ደስታን “ለሚወዱት ምነው?” የሚለውን ግጥም አለላት፡፡
አንድ ቀን የህግ ትምህርት ክፍል ሀላፊ ሀሌሉያን አስጠራው፡፡
“ከፕሬዚዳንት ቢሮ አስቸኳይ ደብዳቤ መጥቶ ነበር”
“ምን የሚል?”
“የትምህርት እድል ነው፤ በሲኒየርነትህ እና ባለህ የትምህርት ዝግጅት ብትወዳደር የምታልፈው አንተ ነህ፤ ግን ደግሞ ሴቶች ይበረታታሉ ይላል ደብዳቤው፡፡” አለው፡፡
ወዲያውኑ የሆነ ነገር ብልጭ አለለት፤ ሀሌሉያ፡፡
“እኔ በቅርቡ የመማር ፍላጎት የለኝም፤ ለምን ሚናን አታናግራትም?” ድምጹ ውስጥ ጥያቄ ሳይሆን ትእዛዝ አለ፡፡
“እኔም የፈለኩህ ምን እንደምትል ልሰማህ ብዬ ነው”
“የኔን ሰምተሃል፤ ሚናን አናግራት” ትእዛዝ ነው አሁንም፡፡
የትምህርት እድሉን ሚና አገኘች፤ በስውዲን ሀገር ለአንድ አመት የሚዘልቅ በሰብአዊ መብት ህግ ላይ የሚሠጥ ስልጠና ነው፡፡ ሚና ስላገኘችው የትምህርት ዕድል ስትነግረው፤ ‘Congra’ አላት አቅፎ፡፡ የትምህርት እድሉን እሱ አሳልፎ እንደሰጣት አልነገራትም፡፡
ታህሳስ ሀያ ዘጠኝ ቀን የሚና የልደት ቀን ነው፡፡ ጥር አንድ ቀን ከባህር ዳር አዲስ አበባ፣ ጥር ሁለት ቀን ደግሞ ከአዲስ አበባ ወደ ስቶክሆልም የምትበርበት ቀን ነው፡፡
ይህን ድርብ በአል ለማክበር ፓፒረስ ሆቴል ተቀጣጠሩ፡፡ ሚና የምትወደው ወይ የምታዘወትረው ጥግ ላይ ተቀመጡ፡፡ ሀሌሉያ ቀደም ብሎ ሁሉ ነገር እንዲዘጋጅ አዞ ነበር፤ ኬክ፣ ሻማ፣ ሻምፓኝ … ሁሉም ተዘጋጅቷል፡፡ ሚና ይህን ሁሉ ጠብቃለች፤ ኬክ፣ ሻማ፣ ሻምፓኝ … አለ፤ የምትወደው ሠውዬ ጥቁር ሙሉ ሱፍ፤ በነጭ ሸሚዝ ለብሷል፤ ለብሶላታል። አምሮበታል፤ ሚና ግን አንድ ነገር በጉጉት እየጠበቀች ነው፡፡ በዚህ ቀን ሰውዬው ምን አይነት ስጦታ እንደሚያበረክትላት ለማየት ጓጉታለች፡፡ እራሷን እስክትታዘብ፣ እስኪያስታውቅባት ድረስ ተቅበጠበጠች፡፡ ሀሌሉያ እጅ ላይ ደግሞ ምንም አይነት ለስጦታ የሚሆን ጥቅል አይታይም፡፡ ይበልጥ ተቅበጠበጠች፡፡ እሷ ለዚህቀ ድንቅ ሠው ዛሬ ልዩ ስጦታ አዘጋጅታለታለች፡፡ ቀይ ስጦታ፡፡
እሱስ? ያ አይደለ እንዴ ታዲያ ጥያቄው፡፡
“እወድሻለሁ” አላት፡፡
“ቀጣፊ፣ ውሸታም!”
“እንዴት እንደምወድሽ ታውቂያለሽ?” አላት እንዴት ነው የምትወደኝ? እንድትለው አማልክቶቹን እየተማፀነ፤ አማልክቶቹ ፀሎቱን ወዲያው ሠሙት፡፡
“እንዴት ነው የምትወደኝ?” አለችው ሚና። ተነስቶ ቆመ፣ ከኪሱ ወረቀት አወጣ፣ በእርጋታ ዘረጋው፡፡
“ክብርት ሆይ ይህ ግጥም ላንቺ በረከት ይሁን ብዬ እራሴ የፃፍኩት ነው”
የሚከተለውን ግጥም አነበበላት፡፡
እንዴት ነው የምወድሽ እንኳ?
እንደ አበቦቹ ሽታ፣
እንደ ቢራቢሮ እስክስታ፣
እንደ ጥርኝ ጭቃ፣
ልክ እንደ ስጦታ እቃ፣
እወድሻለሁ እኔ እወድሻለሁኝ፡፡
እንደ ፍልስፍና ሃሳብ፣
ሊጠግብ እንዳለ ረሀብ፣
እንደ ህፃን ልጅ ሳቅ፣
እንደ ዘላለማዊ ሀቅ፣
እወድሻለሁ እኔ፣ እወድሻለሁኝ፡፡
እንደ ሎጂክ፣
እንደ ተፈጥሮ ህግ፣
እንደ ቋንቋ፣
ልክ እንደ ሙሉ ጨረቃ፣
እወድሻለሁ እኔ፣ እወድሻለሁኝ፡፡
እንደ ሙዚቃ ቅንጣት፣
እንደ አልጋ ውስጥ ትኩሳት፣
ልክ እንደ እናቴ ስም፣
እንደ ልጅነቴ ህልም፣
እወድሻለሁ እኔ፣ እወድሻለሁኝ፡፡
እንደ ግጥም ስንኝ፣
አንጀሎ እንደጠረበው ቋጥኝ፣
እንደ ጠዋት እንቅልፍ፣
እንደ አየር ራንድ ፅሁፍ፣
እወድሻለሁኝ እኔ፣ እወድሻለሁኝ፡፡
እንደ ብርቱካን ውሃ፣
እንደ ብርሃን ዘሃ፣
እጄ ላይ እንደያዝኩት ሲጋራ፣
እንደ ቀዝቃዛ ቢራ፣
እንደ ሊዮናርዶ ስራ፣
እወድሻለሁ እኔ፣ እወድሻለሁኝ፡፡
ፍቅሬ ሁሉን እንደ እርሺ
ይህን እንደ ብቻ ያዢ፤
አፈቅርሻለሁ ነፍሴ፣
ልክ እንደ እራሴ፡፡
ልክ አንብቦ እንደጨረሰ አካባቢያቸው በጭብጨባ ቀለጠ፤ ሁለቱም ደነገጡ፤ የምር ደነገጡ፡፡ ዙሪያቸውን ቢያዩ በቤቱ አስተናጋጆች እና በሆቴሉ ስራ አስኪያጅ ተከበዋል፡፡
“አንድ ጊዜ …” አለ የፓፒረስ ሥራ አስኪያጅ፡- “አንድ ጊዜ፣ የሆቴሉ ሠራተኞች ስጦታ ስላዘጋጀንላችሁ እንድትቀበሉ በላቀ አክብሮት እንጠይቃለን” ድምፁ ውስጥ ፍቅር ነው ያለው፤ ድምፁ ውስጥ እና አኳኋኑ ውስጥ ቅርበት አለ፡፡
ብዙ ጊዜ ሚናን እና ሀሌሉያን የሚያስተናግደው ልጅ፣ ኬክ እና ብላክ ሌብል ውስኪ ከጎናቸው ያለው ጠረጴዛ ላይ አኖረ፡፡ ሀሌሉያ ያዘዘውን ኬክ ሚና እየተጨበጨበላት “Happy Birthday to Mina” እየተባለላት ቆረሰችው፡፡ የሆቴሉ ሠራተኞች ለሁለቱ ያበረከቱትን ኬክ ሀሌሉያ እንዲቆርስ ተጋበዘ፡፡ ከፈተው፡- “ለሚና እና ለቴታ፡- ከፓፒረስ” ይላል፤ ሀሌሉያ ግንባሩን ቅጭም አደረገ፤ ሊና አጠገቡ ናት፤ እሷም እሱን ተከትላ ቅንድቧን ቅጭም አደረገች፡፡
“ቴታ ምን ማለት ነው? ምንድነው?” አሉ ሀሌሉያ እና ሚና አንድ ላይ፡፡
“Tamed Tiger ማለት ነው፤ ያንተ ቅፅል ስም ነው” አለች ፊቷ፣ አንገቷ፣ እና እጆቿ በአረንጓዴ የደም ስሮች የተሞሉ፤ ቀጭን፣ ረዥም፣ ቆንጆ አስተናጋጅ፡፡ ስሙን እሷ እንዳወጣችለት ያስታውቅባታል፡፡
የሬይ ቻርለስ Hallelujah-I Love Her So የሚለው ዘፈን በሆቴሉ ማጫወቻ እየተጫወተ ሀሌሉያ ኬኩን ቆረሰ፡፡ የሬይ ቻርለስ ዘፈን ሲያልቅ የቢሊ ኦሽን Caribbean Queen ቀጠለ፡፡ የሚከተሉትን ስንኞች፡- “In the blink of an eye I knew her number and her name; yeah; She Said I was a Tiger She wanted to tame” ሲሰማ ፈገግ አለ፤ ሀሌሉያ፡፡ Tamed Tiger ያለችውን አስተናጋጅ በአይኑ ፈለጋት፤ አገኛት፤ እየሳቀች አየችው፤ በአይኗ ቀስ ብላ ሳመችው፤ አፈረ፡፡
አሪፍ ፌሽታ ሆነ፡፡
ለሁሉም ከብላክ ሌብሉ ከተቀዳ በኋላ ሀሌሉያ ውስኪውን ከነጠርሙሱ ያዘው፤ በጠርሙሱ ነበር የሚጠጣው፡፡ ሚና ሻምፓኙን ተያይዛዋለች፤ በየመሀሉ የሀሌሉያን ጠርሙስ እያነሳች ትጎነጫለች።
ሞቅታ፡፡
ሚና ከዚህ በፊት እንደዚህ አይነት ደስታ ተሰምቷት አያውቅም፤ ከዚህ የሚልቅ ደስታም አለ ብላ አታስብም፤ ፍፅምና፣ ፅድቅ፣ ከፍታ፣ ልዕልና፣ … ይህ ሁሉ ነው የተሠማት፤ እና ለዚህ ሁሉ ደስታ መነሻ ለሆነው ለአቶ ቴታ፡- “እንዴት ደስ የሚል ቅፅል ስም ነው ግን? እኔንም እሱንም የሚያወድስ ስም ነው፤ እሱ ነብር ነው፤ የገራሁት ደግሞ እኔ፤ አይ መመፃደቅ አበዛሁ መሰለኝ፤ እኔ አይደለሁም ፍቅር ነው የገራው፣ እያለች አሰበች፡፡
ለሀሌሉያ፣ ለተገራው ነብር ስጦታ አዘጋጅታለታለች፤ ቀይ ስጦታ፡፡ ዛሬ አብረው ነው የሚያድሩት፤ አልተባባሉም፤ እንዲያ አልተባባሉም፤ አብረን እናድራለን አልተባባሉም፤ አብረው አድረው አያውቁም፤ ግን ዛሬ አብረው ያላደሩ መቼ ሊያድሩ ነው? ዛሬ አብራው ታድር እና ሲነጋ ሴት ሆና ትነቃለች፡፡ አሪፍ ስጦታ እንደሆነ እርግጠኛ ናት፡፡
እራት አልበሉም ነበር፣ ኬኩን ቀመሡ፣ መጠጡን አጣጣሙት፤ ሀሌሉያ ድሮም ቢሆን ምግብ ላይ ብዙ አይደለም፡፡
“እራት ልጋብዝህ፤ ሰመር ላንድ እንሂድ” አለችው፡፡
ሞቅ ብሎታል ቴታ፡፡
ለብቻው ሲያስብ እንዲህ እያለ ነበር፡- እራት? አዎ፤ እርቦኛል፤ ሰመርላንድ? ለምን እዚያ?
“እዚሁ እንብላ!” አላት ድምጽ አውጥቶ፡፡
“አይሆንም፤ ሰመርላንድ ፒዛቸውን ለጉድ ነው የምወድላቸው” አለችው፡፡
ውሸቷን ነው፣ ከአዲስ አበባ መጀመሪያ ባህር-ዳር ስትሄድ ያረፈችው ሠመርላንድ ነው፤ መኝታቸውን ወዳላቸዋለች፡፡
ዛሬም እዚያ ነው ማደር፡፡
ሰመር-ላንድ ሆቴል ሄደው እራታቸውን ፍቅራቸውን በጉርሻ እየገለፁ፣ በአይኖቻቸው አድናቆት እየተቀባበሉ በሉ፡፡
እሷ እንዲህ ስትል እያሰበች ነበር፣ “ምናለ፤ ባልጐ ባያውቅ ኖሮ?! ልክ እሱ ለኔ የመጀመሪያዬ እንደሆነው ሁሉ፣ እኔም ለሱ የመጀመሪያው ብሆን ኖሮ እንዴት ድንቅ ይሆን ነበር?! በስመአብ ግን ከስንቶቹ ጋር ተኝቷል? … ግን ይተኛ፣ ምርጥ ሰው ነው …”
እሱ በበኩሉ፡- “ቴታ ነው ያሉኝ? ይገርማል … ይህች ነብስ ነገር የሆነች ልጅ ናት የገራችኝ … ሲከታተሉኝ ነበር ማለት ነው? ይገርማል፤ ቴታ? … እኔ ደግሞ ይህቺን ብርሃን የሆነች ልጅ ፊኒክስ ብያታለሁ … እንደ እሷ አይነት በሺህ አመት አንዴ ነው የሚገኘው … ለዚያውም ፊኒክሶች አይወልዱም፤ አይወለዱም፤ እራሳቸውን ከራሳቸው ነው የሚፈጥሩት፤ ለዚያውም በሺህ አመት አንዴ … ሚና ፊኒክስ ናት … አፍቅሬ አላውቅም ነበር … ፍቅር ይሉት ነገር ግን ደስ የሚለው ነገር አለው … በተለይ ከእንደዚህች አይነቷ ጋር ሲሆን የፅድቅ ይሆናል … የዛሬ አመት ከስዊድን ስትመለስ አለምን በሚያነጋግር ሠርግ አገባታለሁ … እስከዚያ እጠብቃታለሁ … አቦ እስከዘላለም እጠብቃታለሁ …”
ግን ገላው ገላዋን ከጅሎ በረሃብ እየተቃጠለ ነው፤ እየነደደ፡፡
“እስከዛሬ ወሲብን አራክሼዋለሁ … አሁን ግን አልስገበገብም … ፈፅሞ አልስገበገብም … እጠብቃታለሁ … ስልጠናዋን ጨርሳ ከስቶኮሆልም ስትመለስ … የሠርግ ዳስ አስጥዬ ነው የምጠብቃት … ከዚያ ብር አምባር ሰበረለዎ፤ ሆሆ ጀግናው ልጅዎ … ይባልልናል … አንድ አመት በጣም ቅርብ ነው፣ እጠብቃታለሁ …”
ግን አሁንም ገላው ገላዋን ከጅሎ በረሃብ እየተቃጠለ ነው፤ እየነደደ፡፡
ሚና በበኩሏ በደስታና በፍርሃት ተውጣለች፡- “…የመጀመሪያው ቀን እንዴት ይሆን?... እንዴትም ይሁን … ሀይለኛ ደስታ ሳይኖረው አይቀርም … ደሞ እኮ ልጁ ሀሌሉያ ነው…”
ሳትነግርው ተነስታ ወደ ሆቴሎ እንግዳ መቀበያ ሄደች፤ አልጋ ተከራየች፤ በመጀመሪያ ባህር-ዳር ስትመጣ ያረፈችበትን ክፍል ነው የተከራየችው፤ ክፍል ቁጥር 113፡፡
ሀሌሉያ የሠውነቱን ረሃብ ስላልቻለ አንድ መላ ዘየደ፤ ወደ ቤቱ መሄድ፤ ሄደ፡፡ ወደ ቤቱ እየተንገዳገደ ሲሄድ በቀስታ እንዲህ እያለ እየዘፈነ ነበር፡-
“… ብር አምባር ሰበረልዎ፣
ብር አምባር ሠበርልዎ
ሆሆ ጀግናው ልጅዎ፤
አለምሽ ዛሬ ነው ዛሬ
ሆሆ! እቴ ሸንኮሬ …”
እዚህ ጋ በሀሳቡ ቆም አለ፡- “…አሃ! አሃ! በመጀመሪያ በሠርግ ያገባችው ድንግል ሙሽራ የወይዘሮ ሸንኮሬ ልጅ ነበረች ማለት ነው …?” ከት ብሎ ሳቀ፡፡ “ይኸው የወይዘሮ ሸንኮሬ ስም እስከዛሬ ሲጠራ ይኖራል፤ የወይዘሮ ሸንኮሬ ልጅ ስሟ ማን ነበር ይሆን…? ሚና እንደሚሆን እርግጠኛ ነኝ…”
እንዲህ እያለ ቤቱ ደረሠ፡፡ ቤቱ እንደደረሰ ጫማውን ብቻ አውልቆ አልጋው ላይ ተዘረረ፤ ወዲያውኑ እንቅልፍ አቀፈው፡፡
ሚና ስትመለስ ሀሌሉያ የለም፤ መታጠቢያ ቤት ሄዶ ይሆናል ብላ ጠረጠረች፣ ብትጠብቅም አይመጣም፡፡ ስልኩ ላይ ደወለች፤ ዝግ ነው፡፡
ጥግ ላይ ቆሞ አትኩሮ የሚመለከታትን አስተናጋጅ ጠራችው፡፡
“እሱስ?!” አለችው፤ ሀሌሉያ ተቀምጦበት የነበረውን ወንበር እየጠቆመች፡፡
“ሄዷል፤ ሂሳብ ከፍሎ ሄዷል” አነጋገሩ ሀሌሉያን በደንብ እንደሚያውቀው ያስታውቃል፡፡
አላመነችም፡፡ ካለማመኗ እና ግራ ከመጋባቷ የተነሳ፡- “እስኪ!” ብላ እጇን ዘረጋች፤ ለአስተጋናጁ እንዲምልላት፡፡
እጇን ግጥም አድርጐ መታት፤ አመታቱ ያማል።
ስልኩ ላይ ደግማ ደወለች፤ ዝግ ነው፡፡ ዝግ መሆኑን እያወቀች ደጋግማ ደወለች፡፡ ዝግ ነው!
ሀሌሉያ ትቶት የሄደውን ውስኪ ከነጠርሙሱ አንስታ አንደቀደቀችው፤ ጠርሙሱ በትንፋሿ ድምፅ እስኪጮህ ድረስ አንጠፈጠፈችው፡፡ አስተናጋጁ በቅርብ እርቀት አለ፤ በምልክት ጠራችው፤ ተጠጋት፤ በእጇ ያለውን ቁልፍ አቀበለችው፤ የቁልፉ ማንጠልጠያ 113 ይላል፡፡
በጥያቄ ዓይን አያት፡፡
“ውሰደኝ” አለችው፡፡ ደጋግፎ አነሳት፡፡ ሠክራለች፤ ሚዛኗን ጠብቃ መቆምም መራመድም አልቻለችም፡፡ ግማሽ አቅፎ፤ ግማሽ ደግፎ ወሰዳት - ወደ 113 ቁጥር፡፡ በአንድ እጁ እሷን ደግፎ በሌላ እጁ የመኝታ ክፍሉን ቁልፉ ከፈተው፡፡
ይዟት ገባ፡፡
ውስጥ ሲገቡ ከእቅፉ ተላቃ እንደምንም ብላ እራሷን ችላ ቆመች፤ ቆሞ ያያታል፡፡
“በሩን ዝጋው”
ዘጋው፡፡
“አታፍጥብኝ፤ ና ዚፔን ክፈትልኝ”
ከማጅራቱ እስከ ወገቧ ያለውን የቀሚሷን ዚፕ ከፈተው፤ እጆቿን ከቀሚሷ ስታወጣ፣ ቀሚሷ መሬት ወደቀ፤ ቀይ ቀሚስ፡፡
ወደ አስተናጋጁ ዞረች፤ ጡቶቿ፤ እዚህ ጋ አንድ የሀገሬ ፀሐፊ ያለውን መዋስ ግድ ነው፤ “ጡቶቿ የመዳይ ክዳን ይመስላሉ”
አስተናጋጁ አፈጠጠባቸው፡፡
“ያዛቸው!” አለችው ሚና፡፡
በቀስታ ያዛቸው፡፡
“በደንብ ያዛቸው”
ጨመቃቸው፡፡
ከዚያ ከንፈር፣ ትንፋሽ፣ ምራቅ፣ ሙቀት፣ ላብ፣ ብርሃን፣ ቃጠሎ፣ ሲቃ፣ ፀጉር፣ ገላ፣ ትኩስ ገላ፣ የሚሞቅ ነገር … ሙቀት፣ ሙቀት ላብ፣ … እሳተ ገሞራ፣ ህመም፣ ደም … ፍሬ፣ እንቁላል፣ ዘር …
ድካም፡፡
እንቅልፍ፡፡
ተፈፀመ፡፡

Published in ልብ-ወለድ
Saturday, 03 August 2013 10:47

ማስነጠስ እና መዘዙ

  • ከባድ ማስነጠስ ለሞት ሊዳርግ ይችላል 
  • የኪስ ቦርሳዎች ለጀርባ ህመም ያጋልጣሉ

 በህዝብ ማመላለሻ ትራንስፖርት ውስጥ በጉንፋን፣ በቲቢና መሰል በትንፋሽ ሊተላለፉ በሚችሉ በሽታዎች የተያዘ ሰው ቢያስነጥስ የበሽታውን ጀርሞች በማሰራጨት ከሁለት እስከ አምስት ደቂቃ ጊዜ ውስጥ በመኪናው ውስጥ ያሉትን መንገደኞች ሁሉ በበሽታው ሊበክል እንደሚችል ይታወቃል፡፡ 

ይህንን የጤና ችግር ለማስወገድም የህዝብ ትራንስፖርቶች ሁልጊዜም መስኮታቸው ክፍት እንዲሆን የጤና ባለሙያዎች ሲመክሩ ይሰማል፡፡ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የቲቢ በሽታን ለመከላከል በሚሰጠው የግንዛቤ ማስጨበጫዎችም “መስኮት በመክፈት ቲቢን እንከላከል” በሚል መሪ ቃል በርከት ያሉ ማስታወቂያዎችንና ዘመቻዎችን ያካሂዳል። ከዚህ በዘለለ ዛሬ ዛሬ በማስነጠስ ላይ አዳዲስ ጥናቶች እና ምርምሮች እየተካሄዱ ውጤታቸውም ይፋ እየሆነ ይገኛል፡፡ በዚህ መሠረትም ማስነጠስ እጅግ ከፍተኛ ህመምና ስቃይ ላለው የአከርካሪ ዲስክ መንሸራተትና ለዲስክ መሰንጠቅ እንዲሁም ለአጥንት መሰበርና ለልብ ህመም ይዳርጋል እየተባለ ነው፡፡

የማስነጠሱ ኃይል እጅግ ከፍተኛ ከሆነም በጭንቅላት ውስጥ የሚገኙ የደም ስሮች እንዲበጠሱ በማድረግ፣ በጭንቅላት ውስጥ ደም ፈሶ የአንጣሹ ህይወት እንዲያልፍ ሊያደርግ ይችላል፡፡
በአገራችን ከሚታዩ የወገብ ህመሞች 80% በላይ የሚሆኑት መነሻቸው የዲስክ መንሸራተት ነው፡፡ የአከርካሪ አጥንት ህክምና ዶክተሩ (ካይሮ ፕራክተር) ዶ/ር ተስፋሁነኝ እንዳለ እንደሚናገሩት፤ በምናነጥስበት ወቅት የሰውነታችን አጠቃላይ እንቅስቃሴ ከቁጥጥር ውጪ ስለሚሆን ጅማቶቻችን ከልክ በላይ ይወጠሩና የጡንቻ መጋጠሚያና ዲስኮች አደጋ ላይ ይወድቃሉ፡፡
የማንጠሱ ኃይል እጅግ ከፍተኛ በሚሆንበት ወቅት የአከርካሪ ዲስኮችን ሊሰነጥቅ፣ ጥርስ ሊያረግፍና ምላስንና የጉንጭ ውስጠኛው ክፍል ሊቀረጠፍ ይችላል፡፡ ችግሩ የጭንቅላት የደም ስሮች እንዲበጠሱ በማድረግ ደም በጭንቅላት ውስጥ ፈሶ የአንጣሹ ህይወት እንዲያልፍ ሊያደርገውም ይችላል፡፡
“በእያንዳንዱ የአከርካሪ አጥንቶቻችን መካከል የሚገኙትና ዲስክ እየተባሉ የሚጠሩት አካላት የተሰሩት ስፖንጅ መሰል ከሆነ የሥጋ ክፍል ነው። እነዚህ ዲስኮች ዋና ተግባራቸው የአከርካሪ አጥንቶችን ለመለያየት እና በአከርካሪዎች መካከል ጤናማ እንቅስቃሴ እንዲኖር ማድረግ ነው። ህብለሰረሰር፣ አከርካሪ አጥንት፣ ዲስኮችና ጡንቻዎቻችን በቅንጅት የሚሰሩት ሥራ ጤናማ ሆነን ለመራመድና ለመቆም እንድንችል ያደርጉናል። እንደ ልባችን ጐንበስ ቀና እንድንል፣ አንገታችንን በፈለግንበት አቅጣጫ ማዟዟር እንድንችል፣ አቋቋማችንና አካሄዳችን የተስተካከለ እንዲሆን ዲስኮች ከፍተኛውን ሚና ይጫወታሉ። እነዚህ ዲስኮች በአደጋ፣ ከባድ ዕቃ በማንሣትና በኃይል በማስነጠስ ተፈጥሮአዊ ቦታቸውን ለቀው ሊንሸራተቱ ወይም ሊሰነጠቁ ይችላሉ፡፡ በዚህ ወቅትም ታማሚው እጅግ ከፍተኛ ለሆነ ስቃይ ሊዳረግ ይችላል” የሚሉት ዶ/ር ተስፋሁነኝ፤ ችግሩ እንደልብ ጐንበስ ቀና ማለት አለመቻል፣ አንገትና ትከሻን በፈለጉበት አቅጣጫ ለማዟዟር መቸገር፣ እንደ ኤሌክትሪክ የሚነዝር ህመም፣ የጡንቻዎች መወጣጠርና የአካል መዛልንም ሊያስከትል እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
ማስነጠስ ድንገታዊና በቅፅበት የሚከሰት ነገር ሲሆን በዚህ ወቅት የሰውነታችን አጠቃላይ እንቅስቃሴ ከቁጥጥር ውጪ ይሆናል፡፡ ለማስነጠስ መነሻ የሚሆኑ ምክንያቶች እነዚህ ናቸው ብሎ መዘርዘሩ አስቸጋሪ ነው ያሉት ዶክተሩ፤ በአገራችን የተለመዱና የማስነጠስ ችግርን ሊያባብሱ የሚችሉ እንደ ሰናፍጭ ያሉ ምግቦች በድንገትና ሳይታሰብ የሚከሰቱ ማስነጠሶችን ሊያመጡ ይችላሉ፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ለጉንፋን፣ ለሳይነስና አፍንጫ ከርካሪ ለሆኑ ችግሮች ዳማከሴን ጨምቆ ውሃውን በአፍንጫ ውስጥ በመክተት እንዲያስነጥስ ማድረግ የተለመደ ጉዳይ ነው፡፡ እነዚህ ነገሮች በማንጠስ ምክንያት ሊከሰቱ ለሚችሉ ችግሮች ሊያጋልጡን ስለሚችሉ ከፍተኛ ጥንቃቄ ልናደርግባቸው ይገባል ሲሉ ይገልፃሉ፡፡
ማንጠሱ ጠንከር ያለና የሰውነት ኃይልን የሚያናጋ አይነት እንቅስቃሴን የሚፈጥር ከሆነ በጭንቅላታችን ውስጥ ያሉ የደም ስሮችና ጡንቻዎች እንዲናጉና እንዲበጠሱ በማድረግ ደም ወደ ጭንቅላታችን ውስጥ እንዲፈስ ያደርጋል፡፡

በዚህ ሣቢያም አንጣሹ ወዲያውኑ ህይወቱ ሊያልፍ ይችላል፡፡ ለማስነጠስ ፈልገን ማስነጠሱ እምቢ ሲለን ወይንም የመጣው ሲመለስ አሊያም እኛው እራሳችን ማንጠሱን ለመዋጥ ወይም ላለማስነጠስ ትግል በምናደርግበት ወቅት በጭንቅላታችን ውስጥ ከፍተኛ ግፊት ስለሚፈጠር ለጆሮ ታምቡር መቀደድ ችግር ሊዳርገን፣ ለደም ስሮችና ለጭንቅላታችን ጡንቻዎች መበጠስና ለጭንቅላት ደም መፍሰስ ምክንያት በመሆን ለሞት ሊያበቃን እንደሚችል ዶ/ር ተስፋሁነኝ ገልፀው፤ ይህንን ችግር ለማስወገድ በማንጠስ ወቅት ከፍተኛ ጥንቃቄ ልናደርግ እንደሚገባን ተናግረዋል፡፡ “ልናነጥስ ስንሞክር ወይንም የማንጠሱ ስሜት ሲመጣ አስቀድሞ ይታወቀናል፡፡ በዚህ ጊዜም ቆመን ከሆነ ቀጥ ብለን በመቀመጥና የሆዳችንን ጡንቻዎት በማጠንከር ማስነጠሱ የሚፈጥረውን እንቅስቃሴ ወይም ንቅናቄ ልናቀዘቅዘው (ልናለዝበው) እንችላለን፡፡ ይህ ደግሞ በማንጠሱ ፍጥነትና ጥንካሬ የሚደርሰውን የመውደቅ አደጋ ሊያስቀርልን ይችላል ብለዋል፡፡
የአሜሪካ የስፓይናል ኦርቶፔዲክ ሰርጀኖች ምርምር ውጤት እንደሚያሣየው፤ የአከርካሪ ዲስኮቻችን በሁለቱ የአከርካሪ ቬርቴብራ መካከል የሚቀመጡ ለስላሣ ትራሶች ሲሆኑ እነዚህ ለስላሣ ትራሶች በወጣትነት ዕድሜ ዘመን ለስላሣና እንደ ልብ ተለጫጭ ሆነው ዕድሜያችን እየገፋ ሲሄድ የመለጠጥ አቅማቸው እየቀነሰ መጥቶ ለአደጋ በቀላሉ ተጋላጭ ይሆናሉ፡፡ በዚህ ወቅት የሚያጋጥም ድንገተኛና ጠንካራ ማስነጠስ እነዚህን ዲስኮች በቀላሉ ሊሰነጥቃቸው ይችላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በማንጠሱ ወቅት ጥርሶች ከተጋጩ ሊረግፉ፣ አጥንቶች ሊሰበሩና ለልብ ህመምም ልንጋለጥ እንደምንችል ምርምሮቹ ያረጋግጣሉ፡፡
በማስነጠስም ሆነ በሌላ ጉዳት ሣቢያ የሚከሰቱ የዲስክ መንሸራተቶች፣ ጥመቶችና የዲስኮች ከተፈጥሮአዊ ቦታቸው መልቀቅ ችግሮች መኖራቸው ሊረጋገጥ የሚችለው ሆርሞግራፊ፣ ሲቲ ስካንና፣ ኤም አይ አር፣ በተባሉ የህክምና የምርምር ዘዴዎች ነው፡፡ በዲስኮች ላይ የሚከሰቱ ጥመቶች፣ መንሸራተቶችና መሰንጠቆች በተለያዩ የህክምና ዘዴዎች ማከምና ለችግሩ ዘላቂ መፍትሔ መስጠት ይቻላል፡፡ መድሃኒቶች፣ ደረቅ መርፌዎችና የቀዶ ህክምና ዘዴዎች ለችግሩ ዘላቂ መፍትሔ ለመስጠት የሚያስችሉ የህክምና አይነቶች ናቸው። በዲስክ መሰንጠቅ ወይም መንሸራተት ሣቢያ የተከሰተን ህመም በማሣጅ ቴራፒ ወይም በሴራጂም ለማስወገድ መሞከሩ የከፋ ጉዳት ሊያስከትል ስለሚችል፣ በቅድሚያ የህክምና ባለሙያዎችን ማማከር እንደሚገባ ዶ/ር ተስፋሁነኝ ያሣስባሉ፡፡
በማስነጠስና በተለያዩ ጉዳቶች ሣቢያ ከሚከሰተው የዲስክ መሰንጠቅ ወይንም መንሸራተት ችግር በተጨማሪ በወንዶች የኋላ ኪስ ውስጥ እንደዘበት የሚቀመጡት የኪስ ቦርሣዎች (ዋሌት) በዳሌ አጥንት ላይ መዛባትን በማስከተል ለጀርባ ህመም እንደሚዳርግ ጥናቶቹ ይፋ አድርገዋል። ይኸው የወንዶች የኪስ ቦርሳ ዋሌት ክብደቱ እየጨመረ በሄደ ቁጥር የሚያስከትለውም ችግር የዛኑ ያህል እየጨመረ እንደሚመጣና ከፍተኛ የአጥንት መዛባት በማስከተል ለጀርባ ህመም ያጋልጣል። እናም ጐበዝ ሁላችንም እንደ ቀላል የምናየውና ከምንም ሣንቆጥር በየዕለቱ የምናከናውነው ማስነጠስ እንዲህ ላለ ከባድ ችግርና ጉዳት ሊዳርገን ይችላል፡፡ እናስ ጥንቃቄ ማድረጉ ሳይሻል ይቀራል ትላላችሁ?

Published in ዋናው ጤና