በአፍሪካ ተወዳዳሪ የሌለው የአትሌቲክ መንደር
አዲስ አበባ በጉም የተሸፈነችበት ዕለት ነበር- ያለፈው ማክሰኞ፡፡ ከአምስቱ የመዲናዋ መውጫ በሮች አንዱ ወደሆነው የሰሜን አቅጣጫ አመራሁ። የሱሉልታ ተራራ አናት በጉም በመሸፈኑ፣ በሶስት እና በአራት ሜትር ሰው ለመተያየት ችግር ነበር። ተራራውን እየወረድን ስንሄድ ጉሙ እየሳሳ ሄዶ “መታጠፊያ” የሚባለው አካባቢ ስንደርስ ከነአካቴው ጠፋ፡፡
ሱሉልታ ከተማ ለመድረስ 10 ኪ.ሜ ያህል ሲቀረኝ የታክሲው ረዳት መኪናውን አስቁሞ “ደርሰዋል” ብሎ አስወረደኝ፡፡ ከዚያም በቀኝም በግራም በእጁ እያመለከተኝ “የእሱ ነው” ብሎኝ ጉዞውን ቀጠለ፡፡ እኔም የተወሰኑ ሜትሮች ከተጓዝኩ በኋላ፣ ከባለ አንድ ፎቅ ዘመናዊ ሆቴል ሰፊ መመገቢያ አጠገብ “ቀነኒሳ ሪዞርት” የሚል አየሁና ለጥበቃ ሰራተኛው የመጣሁበትን ጉዳይ ነገርኩት። ጥበቃው ከሜዳው ውስጥ ወደሚመጡ ሁለት ሰዎች እያመለከተ “ለእነሱ ንገር፤ ይጠሩልሃል” አለኝ። እኔም እንደተባልኩት አደረግሁና አስጎብኝዬ አቶ ቱሉ እስኪመጡ ወደ ሆቴሉ አመራሁ፡፡
ከጥቂት ቆይታ በኋላ አቶ ቱሉ መጡና የመጣሁበትን ጉዳይ ነግሬያቸው ጉብኝቴን ጀመርኩ፡፡ ከወደሰሜን በኩል የእግር ኳስ ሜዳው አርቴፊሻል ሣር ለብሷል፡፡ አረንጓዴነቱ በጣም ያምራል፡፡ አውሮፓ እንጂ በአዲስ አበባ ዙሪያ በገጠሪቱ የኦሮሚያ ልዩ ዞን ውስጥ መሆንዎን ይረሳሉ፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፡፡ በኳስ ሜዳው ዙሪያ የተነጠፈውን የመሮጫ ትራክ ሲመለከቱ ቀለሙ ቀይ ከመሆኑ በስተቀር ሰሞኑን 14ኛው የዓለም አትሌቲክ ውድድር የተካሄደበትን የሞስኮ ሉዝንስኪ ስታዲየም ያስታውሰናል፡፡ ከስታዲየሙ ግራና ቀኝ የርዝመት ዝላይ፣የምድር ዝላይ፣የመሰናክል መሮጫ….ተገንብቷል፡፡
የስታዲየሙ “ካታንጋ” መቀመጫ የአፈር መደብ ሳር እየተተከለበት ነው፡፡ በትይዩው ደግሞ “ክቡር ትሪቡን” ለመስራት የአፈር ቁፋሮ ተጀምሯል፡፡ ከ “ካታንጋ” በስተሰሜን ምዕራብ ብዙ ክፍሎች ያሉት የመፀዳጃና የሻወር ክፍሎች ተዘጋጅተው ፊኒሺንግ ነው የቀረው፡፡ ክረምቱ እንደወጣ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያሟላ የመዋኛ ገንዳም ይገነባል፡፡ የሚያጠግብ እንጀራ… እንዲሉ፣ የቀነኒሳ በቀለ የአትሌቲክስ መንደር ሥራ ሲጠናቀቅ ምን ሊመስል እንደሚችልና እንዴት እንደሚያምር ከወዲሁ መገመት አያቅትም።
የክብር ትሪቡኑ ይሰራበታል ከተባለው ስፍራ ጀርባ በጣም ብዙ ርቀት ከተጓዝን በኋላ የስፖርት መንደሩን ከሌላ የሚለይ የሽቦ አጥር እናገኛለን። አጥሩን አልፈን ስንጓዝ እሳት ማንደጃ ያለው ሰፊ የጋራ ባርና ሬስቶራንት፣ ዘመናዊ ኪችንና ላውንደሪ…ያላቸው አምስት ዘመናዊ የእንግዳ ማረፊያ ቪላዎች እናገኛለን፡፡ ክፍሎቹ ቲቪ፣ቁም ሳጥን፣ ወንበርና ጠረጴዛ፣ ሻወር ቤትና መፀዳጃ….አላቸው፡፡ ከቪላው አረንጓዴ ስፍራ አለፍ ብሎ ሌላ የሽቦ አጥር ታጥሯል። ከአጥሩ ማዶ የማጠናቀቂያ ስራ የቀረው ባለ ሶስት ፎቅ ዘመናዊ የእንግዶች ማረፊያ ህንፃ ይታያል፡፡ ከ80 በላይ ክፍሎች አሉት የተባለው ይህ ህንፃ “በኮንትራክተሩ ድክመት ባይሆን ኖሮ እስካሁን ማለቅ ነበረበት” ብለዋል፤ አስጎብኚዬ አቶ ቱሉ፡፡
የታዋቂው አትሌት የቀነኒሳ የሱሉልታ ኢንቨስትመንት በዚህ ብቻ አያበቃም፡፡ እስካሁን ያየነው ከመንገዱ በስተቀኝ ጠርዝ ያለውን ነው፡፡ ከመንገዱ በስተግራ ጠርዝ ያለውንና ከ3ሺህ ካ.ሜ በላይ ያረፈውን ደግሞ እንቃኝ፡፡
“ቀነኒሳ ሪዞርት” ይላል፤ ባለ አንድ ፎቅ ዘመናዊ ሆቴል መግቢያ በር ላይ የተተከለው ማስታወቂያ። ወጪና ገቢ መኪኖችን በደንብ እንዲያስተላልፍ የተሰራውን ሰፊ በር አልፈው፣ አስፋልቱን ተከትለው ሲሄዱ ወደ ሆቴሉ ይደርሳሉ፡፡ ስላልተመረቀ ብዙ ሰው አላወቀም እንጂ የሪዞርቱ ግንባታ አልቆ ስራ ከጀመረ ሰነባብቷል፤ ስምንት ያህል ወራት ተቆጥረዋል፡፡ ሪዞርቱ ዘመናዊ ከመሆኑም በላይ ሰፊ ሎቢ ባር፣ ሬስቶራንትና ካፌም አለው፡፡ ትኩስ ነገርም ይገኛል፡፡ የገረመኝ ነገር የምግቦቹ ዋጋ ነው፡፡ የአዲስ አበባ ሬስቶራንቶች ከሚያስከፍሉት ዋጋ አይበልጥም፡፡ ቁርስ እንደየዓይነቱ፣ ሰላጣና አትክልት በ30 ብር ገደማ፣ ምሳና እራት ከ43 እስከ 52 ብር ይገኛል፡፡ ትልቁ ዋጋ 65 ብር ነው፡፡
ሎቢ ባሩን አልፈው ሲዘልቁ እንግዳ መቀበያውና ከፊት ለፊት ደግሞ ሰፊ አዳራሽ ያገኛሉ፡፡ አንደኛ ፎቅ ያሉት የተለያየ መጠንና ዋጋ ያላቸው 17 መኝታ ክፍሎች ናቸው፡፡ 800 ብር የሚከፈልበት ትልቁና ሰፊው ክፍል ከአልጋና ቢፌው በተጨማሪ ሁለት ወንበርና ጠረጴዛ፣ ስልክ፣ ቲቪ፣ ቁምሳጥን፣ የገንዳ መታጠቢያና ሽንት ቤት አለው፡፡ ባለ 500 ብር ክፍሎች ደግሞ ትልቁ ክፍል ያሉት ነገሮች የተሟሉላቸው ሲሆን መታጠቢያው ገንዳ ሳይሆን የቁም ሻወር ነው፡፡
ከዋናው በር በስተቀኝ ራቅ ብሎ ከቀርከሃ የተሰራ ትልቅ ጎጆ ቤት አለ - ባህላዊ የምግብ አዳራሽ ነው። አዳራሹ መኻል ላይ ዘመናዊ መጠጥ ለሚፈልጉ ባር አለ፡፡ ጠጅና ሌሎች ባህላዊ መጠጦችም አሉ። አዳራሹ በተለያዩ ስዕሎችና ጌጣጌጦች አምሯል። ንፁህ አየር እየሳቡ መዝናናት ለሚፈልጉ ሰዎች ከአዳራሹ ውጪ ዙሪያውን ሰፊ ስፍራ አለ፡፡ ከፊትለፊት አነስ አነስ ያሉ ስድሰት ጎጆ ቤቶች አሉ። ከአዳራሹ በስተቀኝ በኩል አግድም የተሰራ ቤት አለ- ሥጋ ቤት፣ ኪችን፣ ላውንደሪ፣ ግምጃ ቤት፣ ይዟል። በጀርባው ደግሞ ሽንት ቤትና የሠራተኞች ሻወር አለ፡፡ ከዚህ ቤት ራቅ ብሎ የተለያየ ዘመናዊ የህፃናት መጫወቻ የተተከለበት ስፍራ ሲኖር ግቢው በሞላ አረንጓዴ ሳር ለብሷል፡፡
ከጓደኞቹና ከቤተሰቡ ጋር እንዴት እንደሆነ አላውቅም እንጂ ቁጥብ ነው፤ ብዙ ጊዜ ፈገግታ አያሳይም፡፡ ነገር ግን ሀሳቡን በትክክል መግለፅ ይችላል-የኦሎምፒክና የዓለም ሻምፒዮና የ10 እና 5ሺህ ሜትሮች ሪከርድ ባለቤት ጀግናው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፡፡
ቀነኒሳ ወደ ቢዝነስ የገባው ከአራትና ከአምስት ዓመት በፊት እንደሆነ ይናገራል፡፡ “በተወለድኩበት በቆጂ ከተማ ሬስቶራንትና የተወሰኑ መኝታ ክፍሎች ያሉት የተለያዩ አገልግሎቶች የሚሰጥ አነስተኛ ሆቴል ሰርቻለሁ፡፡ በአሰላ ከተማም ሱቆች፣ ሬስቶራንትና ባር ያለው መጠነኛ ቤት ሰርቻለሁ፡፡ ሱሉልታ የአትሌቲክስ መንደር መስሪያ ቦታ ወስጄ እየተንቀሳቀስኩ ነው፡፡
ለምንድነው የአትሌቲክስ መንደሩ ግንባታ የዘገየው?
የአትሌቲክስ መንደር ግንባታ ፕሮጀክት በጣም ሰፊ ነው፤ እንዲህ በአጭር ጊዜ የሚያልቅ አይደለም። የእኛ አገር ባንኮች ድጋፍ የሚሰጡት ከተማ ውስጥ ነው እንጂ ወጣ ብለው በጋራ መስራት አልለመዱም። ይህም ፕሮጀክቱን ከባድ ያደርገዋል፡፡ ብዙ ፋይናንስ ስለሚጨርስ በራስ ብቻ በአጭር ጊዜ ለመጨረስ ይከብዳል፡፡ አሁን ጥሩ ደረጃ ላይ ነው ያለው እኔ በምፈልገው መልኩ ተሰርቶ ካለቀ ሁሉንም ስፖርት ያካተተ በአፍሪካ የመጀመርያው የአትሌቲክ መንደር ይሆናል፡፡
ብቻህን መሥራት ከከበደህ እንዴት ነው ለማጠናቀቅ ያሰብከው?
ብዙ ሚሊየን ብር ባፈስም ያንን ፕሮጀክት ብቻውን ይጨርሳል ተብሎ መታሰብ የለበትም፡፡ ይህ የስፖርት መንደር የአገር ቅርስ ነው፤ ባንክ ገብቶበት መሥራት አለበት፡፡ ማንኛውንም ፕሮጀክት በራሱ ብር ብቻ የሠራ የለም - የተወሰነ ያህል ከግለሰቡ ወይም ከድርጅቱ፣ አብዛኛው ደግሞ ከባንክ በሚገኝ ብድር (ድጋፍ) ነው፡፡ ስለዚህ ያለው ነው፤ የሌለው ነው ተብሎ መታየት የለበትም፡፡ ሚሊየነርም ቢሆን ከባንክ ጋር አብሮ ነው የሚሠራው፡፡ እኔ ብዙ ብር አውጥቻለሁ፤ አሁን ደግሞ ፕሮጀክቱን ለፍፃሜ ለማብቃት አብረውኝ የሚሰሩ ባንኮች መኖር አለባቸው እላለሁ፡፡ ምክንያቱም ይኼ ስፖርት ነው፤ ስፖርት ደግሞ መሰረተ ልማት ነው፡፡ ይህ የስፖርት ማዘውተሪያ ተሰራ ማለት ለአገር የሚጠቅሙና የአገራቸውን ስም በአደባባይ የሚያስጠሩ ምርጥና ብቁ ስፖርተኞች ይፈልቁበታል ማለት ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ነው መታየት ያለበት፡፡
አትሌቲክ መንደሩ ምን ምን ይዟል?
መሰረታዊ የሚባሉ የስፖርት ነገሮች በሙሉ አሉት፡፡ ባስኬትቦል፣ ዋና፣ የተለያዩ የሩጫ ዓይነቶች፣ ጎልፍ፣ የሜዳ ቴኒስ መጫወቻ፣ የልጆች መጫወቻ፣ ደረጃውን የጠበቀ ሆቴል…አካትቷል፡፡
እንዴት ነው በአፍሪካ ደረጃ ያወዳደርከው?
እኔ እንግዲህ በአፍሪካ ውስጥ በመንግሥት ደረጃ ካልሆነ በስተቀር በግለሰብ ደረጃ በስፖርተኛ የተሰራ የለም፣አላየሁም፡፡ የዚህን ዓይነት የአትሌቲክ መንደር በአፍሪካ ቀርቶ በዓለምም በኦሎምፒክ ነው እንጂ በአንድ ስፖርተኛ የተሰራ የለም፡፡ በሌላ ኢንቨስትመንት ሊሳተፉ ይችላሉ እንጂ እንዲህ ለትውልድ በሚተላለፍ የስፖርት መንደር በዓለም ላይ ኢንቨስት ያደረገ ማንም የለም፡፡ ምናልባት በመንግሥት ደረጃ መጠነኛ የስፖርት ማዕከላት ሊኖሩ ይችላሉ፡፡
ይህን የመሰለ ማዕከል የመገንባት ሐሳብ ከየት መጣ?
በአፍሪካ ለመወዳደር ፈልጌ ሳይሆን በዓለም ላይ በአውሮፓና በአሜሪካ ስዘዋወር ሆቴል ያለው፣ ብዙ የስፖርቶች ዓይነት ማስተናገድ የሚችል የስፖርት ማዘውተሪያ ቦታዎች በማየት ነው እዚህ ውስጥ የገባሁት፡፡
በዚህ ቦታ የተለያዩ ስፖርተኞች ሊሰሩ ይችላሉ። ለስፖርተኛ ብቻ ሳይሆን ማንኛውም ሰው በሳምንት መጨረሻ ስፖርት እየሰራ የሚዝናናበት ቦታ በአገራችን ብዙም አልተለመደም፡፡ ስፖርት በሁሉም የዕድሜ ክልል ላለ ሰው አስፈላጊ ስለሆነ የሚቆም አይደለም፤ ከትውልድ ትውልድ እየተቀጣጠለ የሚሄድ ነው፡፡ በሁሉም የዕድሜ ክልል ያሉትን ማሳተፍ በጣም ተመራጭ ያደርገዋል፡፡ እነዚህንና ሌሎችንም ነገሮች በማሰብ ነው ወደዚህ ኢንቨስትመንት የገባሁት፡፡
አሁን’ኮ በየክልሉ ብዙ ስታዲየሞች መሰራት ጀምረዋል?
አዎ! በሌላ አገር በስፖርት ላይ የሚታየው ነገር በእኛ አገር የለም፡፡ አውሮፓ ለውድድር በምሄድባቸው የተለያዩ አገራት መሮጫ ትራክ በየቀበሌው አለ ማለት ይቻላል፡፡ በውጪው ዓለም የእግር ኳስ መጫወቻና መሮጫ ሜዳ በቅርብ ርቀት ይገኛሉ፡፡ በእኛ አገር ገና አሁን ነው እየተንቀሳቀሱ ያሉት እንጂ ከዓመት በፊት በኢትዮጵያ ውስጥ አንድ የመሮጫ ትራክ ነበር ያለው፡፡ ይህ ደግሞ ለሁሉም በቂ አይደለም፡፡ ከሁለት ሚሊዮን በላይ ሰው ለሚኖርባት አዲስ አበባ፣ ከአራት በላይ የስፖርት ማዘውተሪያ ቦታ ሊኖራት ይገባል። ያለበለዚያ ጥቂት ሰዎች ብቻ ናቸው መጠቀም የሚችሉት፡፡ ብዙ ሰው የሚጠቀምበት ከሆነ የስፖርት ማዘውተሪያው ስፍራ ቶሎ ሊበላሽ፣ ቶሎ ሊያረጅ ... ይችላል፡፡
አንድ ሰው በግልም ሆነ በቡድን በሱሉልታው የስፖርት ማዘውተሪያ ለመጠቀም ምን ማሟላት አለበት?
ምንም የተለየ መስፈርት የለውም፡፡ ሰው እዚያ ሄዶ በግልም ሆነ ከልጆቹና ከቤተሰቦቹ ጋር አልጋ ይዞ አርፎ ስፖርቱን ሰርቶ፣ የገጠሩን ንፁህ አየር እየሳበ ሳምንቱን ሙሉ በሥራ የተጨናነቀ አዕምሮውንና አካሉን ዘና ማድረግ ይችላል፡፡ ማንኛውን ሰው እዚያ ሄዶ ሻይ እየጠጣ፣ ንፁህ አየር እየሳበ መዝናናት ይችላል፡፡
ሪዞርቱ በአሁኑ ወቅት ስንት አልጋዎች አሉት?
በአሁኑ ወቅት አገልግሎት እየሰጡ ያሉት 25 ክፍሎች ናቸው፡፡ አሁን ፊኒሽንግ ብቻ የቀረው ባለ ሶስት ፎቅ ህንፃ አለ፡፡ እሱ ተጠናቆ አገልግሎት ሲጀምር 150 ያህል አልጋዎች ይኖሩናል፡፡
ይህን የስፖርት ማዘውተሪያና ሪዞርት ለመስራት ያነሳሳህ ምንድነው?
ማንም ሰው አቅም ካለውና ማድረግ ከቻለ አንድ ነገር መስራት አለበት፡፡ እኔም አትሌቲክስ ላይ ብቻ መሳተፍ የለብኝም፡፡ ሌላ ነገር ላይ በመሳተፍ ለአገሬ የሚጠበቅብኝን ማድረግ አለብኝ፡፡ ለአገሪቱ ትልቅ ገፅታ የሚገነባና ለወገኖቼም የሥራ ዕድል የሚፈጥር ነገር መስራት አለብኝ፡፡ ይኼ ትልቅ ኢንቨስትመንት ነው፡፡ በሩጫ ያገኘሁትን ገንዘብ ዝም ብሎ ማስቀመጥ ሳይሆን ኢንቨስት ማድረግና ማባዛት አለብኝ፡፡ አንድ ሰው ባንክ አስቀምጦ ቢቆጥብም ያው አንድ እንጀራ ነው የሚበላው፤ ቤተሰቡን የሚያስተዳድርበት አያጣም፡፡ በአንድ ካፌም መኖር ይችላል፡፡ የእኔ ግን ከዚያ በላይ ነው፤ የአገር ገፅታ መገንባትና ለወገኖቼ የሥራ ዕድል መፍጠር፡፡
እስካሁን ድረስ ምን ያህል ብር ኢንቨስት አድርገሃል?
ስላልደመርኩት እስካሁን ይህን ያህል ብር ኢንቨስት አድርጌአለሁ ማለት አልችልም፡፡ በአገር ቤት (በቆጂ)፣ በአሰላ፣ በአዲስ አበባና በሱሉልታ ኢንቨስት ያደረግሁት ቢቆጠር በመቶ ሚሊዮን የሚገመት ብር ነው፡፡
ለምን ያህል ሰዎች የስራ ዕድል ፈጥረሃል?
ስራው ገና አላለቀም፤ ሲያልቅ ብዙ ሰራኞች ያስፈልጋሉ፡፡ እስካሁን በክልል፣ በአዲስ አበባና በሱሉልታ ያሉ 300 ይሆናሉ፡፡
ባለ 4 ኮከቡን ሰው መክሮህ ነው ወይስ ምን አይተህ ጀመርክ?
ማንንም አላማከርኩም፡፡ በኢንቨስትመንት መሳተፍ ደስ ይለኛል፡፡ አዕምሮዬ ያዘዘኝን ለማድረግ ፈልጌ ነው፡፡
ለወደፊት ያሰብካቸው ኢንቨስትመንቶች አሉ?
አዎ! በአዳማ ከተማ ሲኒማ ቤትና የተለያዩ ሱቆች ያሉት የገበያ ማዕከል ተጀምሯል፡፡ ነገር ግን ከኮንትራክተሩ ጋር ስላልተግባባን ስራው ቆሟል፡፡ የተፈጠረው ችግር ሲወገድ ግንባታው ይቀጥላል፡፡ ሁለት ትላልቅ ፕሮጀክቶች አልተጠናቀቁም፤ ጅምር ላይ ነው ያሉት፡፡
አንተ አትሌት ነህ፡፡ ልምምድ አለ፣ ውድድር አለ፤ ከኢንቨስትመንቱ ጋር ሲሆን አያስቸግርህም?
ማንኛውም ሥራ አልጋ በአልጋ ሆኖ የምትመራው አይደለም፡፡ ሥራ ከተባለ የራሱን ጊዜ ሰጥተኸው አስበህ ነው መስራት ያለብህ፡፡ ሁሉም ስራ ለሌላው ሰው ሰጥተህ የምትተወው አይደለም። ገንዘብ እስከወጣበት ድረስ ተቆጣጣሪ ቢኖረውም መከታተል ግድ ይላል፡፡ ሥራውን እንዲመሩ እውቀትና ልምድ፣ የተማሩና አቅም ያላቸውን ሰዎች ነው ያሰማራሁት፡፡ በእርግጥ ቀላል አይደለም። ግን ያስቸግረኛል ብዬ የምሰጋበት ነገር የለም፡፡ በየትኛውም ዘርፍ ውጣ ውረዶች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ይኼ ደግሞ በጥረትና በብልጠት ይታለፋል፡፡
እስካሁን በጣም ፈታኝ ነው የምትለው ችግር (ቻሌንጅ) ምንድነው?
የአዲስ አበባውን ሆቴል ስሰራ በጣም ፈታኝ የሆኑ ችግሮች አጋጥመውኛል፡፡ በግንባታው ላይ ባለመግባባት ብዙ ኮንትራክተሮች ተቀያይረውበታል፡፡ ይህ ስራ እንዳሰብኩት አለመሄዱ ትልቅ ችግር ነበር፡፡ የሆቴሉ ግንባታ አምስት ዓመት ስለፈጀ ቶሎ ስራ ለመጀመር ተፅዕኖ ፈጥሮብኛል፡፡ ምክንያቱም አንድ ኢንቨስትመንት በተፈለገው ጊዜ አልቆ ስራ ካልተጀመረ ኪሳራ ነው። ብዙ ገንዘብ አንቆ ስለሚቀመጥ ወጪው ይበዛል፡፡
ከኮንትራክተሮቹ ጋር ያለው ችግር ምንድነው?
አብዛኛውን ጊዜ ከእነሱ ጋር ያለው ችግር ያሉትን ሆነው ያለመገኘት ነው፡፡ ምናልባት ከመጀመሪያውኑ አስበው የሚገቡበት ነገር ይኖራል፡፡ ያ ነገር ሳይሳካላቸው ሲቀር፣ ተስፋ ቆርጠው (ዲስከሬጅ በመሆን) ስራውን ማጓተት፡ እልህ መጋባት ይፈጠራል፡፡ በኮንስትራክሽን ዘርፍ ጥሩ የሚሠሩ ኮንትራክተሮች የመኖራቸውን ያህል እንጀራችን ነው ብለው ለፕሮፌሽኑ ተጨንቀው የማይሰሩ ሰዎች ይኖራሉ፡፡
በቀረበው መስፈርት መሰረት ከተዋዋለና ገንዘቡን ከተቀበለ በኋላ፤ ኃላፊነቱን ይተውና ሌላ አነስተኛ ችሎታ ያለው ሰው ቀጥሮ ስራውን ይሰጠዋል። ችሎታ የሌለው ሰው ስራህን ሲያበላሽብህ ዝም ብለህ አትመለከተውም-ታስቆመዋለህ፡፡ የችሎታ ማነስም አለ፡፡ “እንችላለን” ብለው ይገባሉ፤ስራው ከአቅማቸው በላይ ሲሆን ችግር ይገጥማቸዋል፡፡ “ለምን እንዲህ አደረክ?” ተብለው ሲጠየቁ፣ ስህተትና ድክመታቸውን አይቀበሉም፤ አውቀውም ወይም ሳያውቁም ሊሆን ይችላል፤ ራሳቸውን ትክክለኛ አድርገው ይከራከራሉ፡፡ “ጥፋተኛ ነኝ ካልኩ ኪሳራ ይደርስብኛል” በማለት ስህተታቸውን ይክዳሉ። ጥቂት ለፕሮፌሽኑ ያደሩ ደግሞ ስህተታቸውን አምነው ተቀብለው ያርማሉ፡፡
እንዲህ ዓይነት ችግሮች ሲያጋጥምህ እንዴት ነው የምትፈታው? ፍርድቤት ትሄዳለህ?
እንደሁኔታው ነው፡፡ ፍ/ቤት ሄጄ የማገኘው ጥቅምና ጉዳት ምንድው? ብለህ ታስባለህ፡፡ ፍ/ቤት መቆም ካለብህ ትቆማለህ፡፡ አለመግባባት ተፈጥሮ ያንን መወጣት ካልቻለ፣ ውል ማፍረስ ስለሚቻል ጥሎ ይሄዳል፤አንተም ሌላ ሰው መቀየር ትችላለህ። “በገባው የጊዜ ገደብ ውስጥ ጨርሶ አላስረከበኝም” ብለህ ፍ/ቤት ብትሄድ ተጨማሪ ወጪ ታወጣለህ፤ ጊዜ ታባክናለሁ፤ ራስ ነህ የምትጎዳው፡፡ ስለዚህ እርቅ ወይስ ፍ/ቤት መሄድ ይሻላል? ብለን አስበን ነው የምንወስነው፡፡
የአዲስ አበባውን ሆቴልና የሱሉልታውን ሪዞርት በስምህ ነው የሰየምከው፡፡ ስምህን ብራንድ ለማድረግ ፈልገህ ነው?
አዎ! ሰው መጠቀም ያለበት ባለው ነወ፡፡ እኔም በስፖርቱ (በሩጫው) ያፈራሁት ዝና አለ፡፡ ብዙ ደጋፊዎች፤ በሰራሁት ሥራ የሚደሰቱ ብዙ ሰዎች ስላሉ ይህንን ስም ብጠቀም ብዙ ማስታወቂያ መሥራት ሳያስፈልገኝና ሳልጨናነቅ በእነዚህ ሰዎች መተዋወቅ እችላለሁ፡፡ አንድን ሥራ በስምህ ማድረግ ደግሞ ትልቅ ነገር ነው እንጂ መጥፎ አይደለም፡፡ በስምህ ስታደርገው ታሪክ ነው የምታስቀምጠው። የሰው ልጅ ያልፋል፡፡ በስምህ የተከልከው ግን ከትውልድ ትውልድ እየተላለፈ ይኖራል፡፡
ይኼ ባለ 4 ኮከብ ሆቴል ምን ምን አለው?
በሆቴሎችና ቱሪዝም መስፈርት መሰረት፣ ለእንግዶች አስፈላጊ የሆኑና መሟላት ያለባቸውን መሰረታዊ ነገሮች አሟልቶ ይዟል፡፡
ባለ 4 ኮከብ ሆቴል መዋኛ፣ የተለያዩ መጠን ያላቸው አዳራሾች፣ የቤት ውስጥና ከቤት ውጭ ስፖርቶች… ሊኖሩት ይገባው ይመስለኛል፡፡ እነዚህን ነገሮች ሳያሟላ ባለ 4 ኮከብ ማለት ይቻላል?
5 ኮከብ ሲሆን ነው እንጂ 4 ኮከብ ላይ እነዚህን ነገሮች ማካተት ግዴታ አይደለም፡፡ 4 ኮከብ ሆቴል የስፖርት ማዘውተሪያ ይኑረው የሚል ሕግ የለም። መዋኛ አስፈላጊ ሊሆን ይችላል፡፡ ይህን ደግሞ በማስፋፊያ እናካትታለን፡፡ የተባሉትን ነገሮች በሙሉ ብናሟላ ወደ 5 ኮከብ ከመሄድ የሚያግደን ነገር የለም፡፡ የሚጨምረውም ወጪ ይህን ያህል ከባድ አይደለም፡፡ ዋናው ችግር ቦታው በቂ አይደለም። በ3ሺ ካ.ሜ ላይ እነዚህን ሁሉ ነገሮች ማካተት በጣም ማጨናነቅ ነው የሚሆነው፡፡
በማስፋፊያው ምንድነው የሚጨመረው?
አሁን ያለን አነስ ያለ አዳራሽ ነው፡፡ ወደፊት ትልቅ አዳራሽ ይኖረናል፡፡ የመዋኛ ገንዳ፣ ተጨማሪ ክፍሎችና የቅርፃ ቅርፅ መሸጫ ሱቆች… ናቸው፡፡
በዓለም ደረጃ ታዋቂ የሆኑ አትሌቶች በአገራቸው ኢንቨስት ያደርጋሉ?
ኬንያዊያን ያደርጋሉ፡፡ አንዳንዶቹም ጓደኞቼ ስለሆኑ በእርሻ፣ በስፖርት ካምፕ፣ በሆቴል ቱሪዝም ላይ ሲሳተፉ አያለሁ፡፡ ስለሌሎች አገር አትሌቶችን ግን ምንም መረጃ የለኝም፡፡ ይሳተፉ ይሆናል፣ ግን በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚታወቅ ነገር የለም፡፡
ዓለም አቀፍ ታዋቂ አትሌት ነህ፡፡ እንዳንተ ያሉ አትሌቶች ደግሞ ስፖንሰር አላቸው፡፡ ያንተ ማን ነው?
ናይክ ነው፡፡
ለምን ያህል ጊዜ?
የ10ሺ እና የ5ሺ ሜትር የኦሎምፒክና የዓለም ሻምፒዮና ክብረወሰን በእጄ ነው ያለው፡፡ በ10ሺ ሜትር ከ10 ዓመት በላይ፣ በ5ሺሜ ደግሞ ከ7 ዓመት በላይ ናይክ ስፖንሰር አድርጐኛል፡፡ እነሱ የሚያተኩሩት ወቅታዊ ብቃት ላይ ነው፡፡ እኔ ደግሞ ከሦስት ዓመት በላይ እግሬን ታምሜ ብቃቴ ቀንሷል። ናይክ ከእኔ ጋር ይቀጥል አይቀጥል እንደሆነ ወደፊት እናያለን፡፡
ስፖንሰርሺፕ የሚያስገኘው ጥቅም አለ እንዴ?
አይ! የለም፡፡ ስም ብቻ ነው፡፡
ቀነኒሳ ምን አይነት ሰው ነው? ምን ይወዳል? ምን ይጠላል?
እንግዲህ ስለእኔ ባህርይ መናገር የሚችለው የሚያውቀኝና የሚቀርበኝ ሰው ነው፡፡ እኔ እንደዚህ ነኝ ብዬ መናገር ይከብደኛል፡፡ ጥሩ ነገሮችን እወዳለሁ፤ መጥፎ ነገሮችን እጠላለሁ፡፡ ያለኝን አካፍዬ መኖር የምፈልግ ሰው ነኝ፡፡
ከምግቦችስ?
የሰው ልጅ ለምግብነት የሚጠቀማቸውን አልጠላም፡፡ ሁሉንም አይነት ባይሆንም አብዛኛውን እጠቀማለሁ - የምጠላው ነገር የለም፡፡ የሰው ልጅ ዛሬ የሚፈልገውን ምግብ ሲያገኝ ነገ ደግሞ ሊያጣ ይችላል፡፡ የምፈልገውን ሳላገኝ ስቀር “ገንዘብ ስላለኝ ይህንን አልበላም” ማለት የለብኝም፡፡ የተገኘውን አክብሬ መቀበል አለብኝ፡፡ ተገልዬ መኖር አልችልም።
ስንት ዓመትህ ነው?
አሁን 31 ዓመቴ ነው፡፡
ስንት ልጆች አሉህ?
ሦስት ልጆች አሉኝ፡፡
ከባለቤትህ ጋር ያለህ ግንኙነት ምን ይመስላል? ሠራተኛ ናት ወይስ የቤት እመቤት?
የምናደርገውን ነገር ተመካክረንና ተነጋግረን ነው የምንሠራው፡፡ ልጆቹንም ታሳድጋለች፤ መሥራት ያለባትንም ነገር ትሰራለች፡፡ ልጆች የማሳደግ ሥራ ከባድ ነው፡፡ የቤት ውስጥና የውጭ ሥራ ቀላል ነገር አይደለም - ከባድ ነው፡፡ በሁሉም ነገር ትደግፈኛለች፤ አብራኝም ትሳተፋለች፡፡ ስለዚህ የጀርባዬ አጥንት ናት ማለት እችላለሁ፡፡

 

“ጠ/ሚኒስትርነት ምቾትም ነው፤ እስርቤትም ነው”
የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከሞቱ መንፈቅ ሞላቸው አይደል (ጊዜው እንዴት ይከንፋል!) እሳቸውን ተክተው እንዲመሩን ኢህአዴግ የሾማቸው ጠ/ሚኒስትር ኃ/ማርያም ደሳለኝ ደግሞ በአዲሱ ዓመት ሥልጣን ከያዙ መንፈቅ ይሞላቸዋል፡፡ (ዓመት ገዙን ማለት እኮ ነው!) በነገራችን ላይ የመለስ ሙት ዓመት በችግኝ ተከላ መታወሱ አስደስቶኛል፡፡ (የአረንጔዴ ልማት ተሟጋች ነበሩ እኮ!) የአካባቢ ጥበቃ ቡድን ጭፍን ደጋፊ ግን አልነበሩም፡፡ የግድቡን መገንባት የተቃወሙትን ምን እንዳሏቸው እናስታውሳለን፡፡ እናላችሁ … ችግኝ ተከላው ጥሩ ሆኖ ሳለ አንድ ሃሳብ ግን አለኝ፡፡ ለሳቸው ሙት ዓመት በመላ አገሪቱ የተተከለውን የችግኝ ብዛት መተሳሰብ ያለብን ይመስለኛል፡፡ (የአገር ሃብት እኮ ነው!) በ2000 ዓ.ም የሚሊኒየሙ በዓል ጊዜ ተተክለው የነበሩ ችግኞች ይፅደቁ ይክሰሙ የምናውቀው ነገር የለም እኮ! (መረጃ የለንማ!) እርግጠኛ ነኝ ለመለስ የአንደኛ ዓመት መታሰቢያ የተተከሉት ችግኞች በዕድላቸው ይፅደቁ የምንላቸው አይደሉም (የአበሻ ልጅ ነው በእድሉ ያድጋል የሚባለው!) ስለዚህ ለከርሞ “የችግኝ ተከላው ሰምሯል አልሰመረም?” የሚለውን በመረጃ ላይ ተመስርተን እንድንገመግም የችግኞቹ ብዛት አሁኑኑ ይነገረን፡፡ (ለሃሜት በር ላለመክፈት እኮ ነው!) የጠ/ሚኒስትሩ ሙት ዓመት የተዘከረው ግን በችግኝ ተከላ ብቻ እንዳይመስላችሁ፡፡ በዲስኩርም በግጥምም የዘከሩ አሉ፡፡ (ለካ የካድሬ ግጥም አይጥምም!!)
ትንሽ ያልተመቸኝ በመፈክር የታጀበው አዘካከር ነበር፡፡ ካልተሳሳትኩ የአዲስ አበባ መስተዳድር በመፈክር ነው ሙት አመቱን የዘከረው፡፡ እኔ እስከማውቀው ድረስ ደግሞ መለስ የመፈክር ሰው አልነበሩም (በታጋይነታቸው አልወጣኝም) አራት ኪሎ ከገቡ በኋላ ግን መፈክር ሲሉም ሆነ ሲያስብሉ አላየንም (ጦሳቸውን!) እናላችሁ … የመፈክር ጋጋታው ከየት እንደመጣና ለምን እንዳስፈለገ ግርም ብሎኛል (ኢህአዴግ አብሾ አለበት እንዴ?) ምናልባት እኮ ለዶ/ር ነጋሶ “መሳቢያ ውስጥ ከተነዋል” ያላቸውን “ሶሻሊዝም” አውጥቶት እንዳይሆን ሰግቼ እኮ ነው (መፈክር የሶሻሊዝም ጣጣ ነው!) ወዳጆቼ… እኛ እንደ ዶ/ር ነጋሶ መታለል አንፈልግም፡፡ (እሳቸውም ግን ወደው አይደለም!) እኔ የምለው ግን ኢህአዴግ “ነጭ ካፒታሊዝም ነው የምከተለው” ሲል አልነበር እንዴ? (እሱማ ድሮ ቀረ!) ዛሬማ “ኢህአዴግ ነፍሴ” የልማታዊ መንግስት ቀንደኛ አቀንቃኝ ሆኖልናል፡፡ ለነገሩ እኛ ነን ያስቸገርነው እንጂ ወዳጅ አገራት ዘንድማ ዝነኝነት አትርፏል፡፡ (ለዚህ እኮ ነው “በአፍሪካ ኢህአዴግን የሚወዳደር ፓርቲ የለም” የተባለው!)
እኔ ግን ሁሌም ግራ የሚገባኝ ምን መሰላችሁ? የአብዮታዊ ዲሞክራሲና የልማታዊ መንግስት አንድነትና ልዩነት? አንዳንዴ ምን ይመስለኛል መሰላችሁ? አብዮታዊ ዲሞክራሲ የልማታዊ መንግስት የቤት ስም! አንዳንዴ ደግሞ የሶሻሊዝም ከፍተኛ ደረጃ ኮሙኒዝም ነው እንደሚባለው የአብዮታዊ ዲሞክራሲም ከፍተኛ ደረጃ ልማታዊ መንግስት ይመስለኛል፡፡ (ነገሩ አልሸሹም ዞር አሉ ነው!) የልማታዊ መንግስት ዋና መለያው ኢኮኖሚው ውስጥ “አትርሱኝ” ማለቱ ነው አይደል? (እንድታስረዱኝ እኮ ነው!) ኢህአዴግ፤ “መንግስት አገር ያስተዳድር እንጂ ኢኮኖሚው ውስጥ ገብቶ “መቀወጥ” የለበትም” የሚሉ ወገኖችን ምን እንደሚላቸው ታውቃላችሁ? “ሞኛችሁን ፈልጉ!”
የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር አንዴ ስለዚህ ጉዳይ ሲናገሩ፤ መንግስት የዘበኝነት ሚና ብቻ እንዲኖረው (ኢኮኖሚው ውስጥ የማይገባ ህግ አስከባሪ!) የሚፈልጉት የኒዮሊበራል አስተሳሰብ አቀንቃኞች እንደሆኑ አስረግጠው መግለፃቸው ትዝ ይለኛል፡፡ (አንዳንድ ካድሬዎች “አገር ለማስተዳደር እንጂ ለዘበኝነት አይደለም የታገልነው” ብለዋል አሉ?)
በነገራችሁ ላይ ባለፈው ዓመት ጠ/ሚኒስትሩ ከሞቱ በኋላ አንድ የቻይና ፊት ያላቸው ምዕራባዊ ምሁር ስለመለስ ጉደኛ ነገር ተናግረዋል፡፡ እራሱ ኢህአዴግም የማያውቀውን! “ዓለም የመለስን የኢኮኖሚ መርህ (የመንግስት እጅ ያለበትን ማለት ነው) ቢከተል ኖሮ ከዓለምአቀፉ የኢኮኖሚው ቀውስ ይድን ነበር” ብለዋል ምሁሩ፡፡ (ነፃ ገበያ ቀለጠ!) እርግጠኛ ነኝ የእኚህ ምሁር አባባል ራሳቸው ኢህአዴጐችንም ሳያስደነግጣቸው አልቀረም፡፡ (እንዲህ አስበው አያውቁማ!) እውነቴን እኮ ነው … መለስ ዓለም አቀፉን የኢኮኖሚ ቀውስ ይታደጋሉ የሚለውን ማንም አስቦትም አልሞትም የሚያውቅ አይመስለኝም፡፡ (ቢያውቁማ ይነግሩን ነበር!) ሌላው ቀርቶ ኢህአዴግ መለስን… “የላቀ አዕምሮ ባለቤት”፣ “የፖለቲካ ሊቅ”፣ “የኢኮኖሚ ምሁር”፣ “የዲሞክራሲ ቀንዲል” … ወዘተ እያለ ማድነቅ የጀመረው የውጭዎቹ ወዳጆቻቸው ተናግረው ሲበቃቸው እኮ ነው! ስለዚህ ልክ እኛ ሲሞቱ “አናውቃቸውም ነበር” እንዳልነው ሁሉ ኢህአዴግም እንዲሁ የተቆጨ ይመስለኛል፡፡

በነገራችን ላይ ስንት ዓመት አብረዋቸው የታገሉ የትግል አጋሮቻቸው እንኳን መለስን እንደፈረንጆቹ አልገለጿቸውም (አያውቋቸውማ!) በዚህ የተነሳም ፓርቲው የውጭ ሰው ስለመለስ እንዲናገር ወይም እንዲመሰክር ላለመጋበዝ ወስኗል የሚል “ሃሜታ” ሰምቻለሁ፡፡ (ከጳጳሱ በላይ ካቶሊክ ሆኑባቸዋ!) ባለፈው ዓመት ፕሮፌሰር ይስሃቅ፤ መለስ እንዳረፉ የተናገሩት ነገርም ከኢህአዴግ እውቀት ውጭ ይመስለኛል፡፡ (የማናውቀውን ስብዕናቸውን እኮ ነው የነገሩን!) በዚህ አጋጣሚ ኢህአዴግ የአሁኑን ጠ/ሚኒስትርና ከፍተኛ አመራሮች ማንነት (ስብዕና፣ ብቃት፣ ፍልስፍና ወዘተ) መርምሮ በቅጡ ቢጠቀምባቸው ይበጀዋል እላለሁ (አሁንም እንዳይቆጭ እኮ ነው!)
እንግዲህ ሰሞኑን የመለስ ሙት ዓመት በችግኝ ተከላ የተዘከረው የችግኝ ፍቅር ስለነበራቸው አይደለም፡፡ ለአረንጔዴ ልማት በዓለም አቀፍ መድረክ ያደረጉትን አስተዋጽኦ ለመዘከር ተብሎ ነው፡፡ እግረመንገዴን መለስ “አረንጓዴ ልማት” ሲሉ ምን ማለታቸው እንደሆነ በቅጡ መረዳት እንዳለብን ማስታወስ እፈልጋለሁ፡፡ (ዕውቀታችን ጥራዝ ነጠቅ ሆኖ ነገር እንዳናበላሽ!)
እኛ ደግሞ በዚህ አምድ አንዳንድ ንግግራቸውን እያስታወስን ትንሽ ብንዘክራቸውስ፡፡ (የአቅማችንን ያህል ማለቴ ነው!) እኔ የምለው…ፓርላማው ኮስተር ብሎ ሥራ የጀመረው የሳቅ ድርቀት ስላጠቃው ነው እንዴ? (ጥያቄ እንጂ ሽሙጥ አይደለም!)
ሰሞኑን ከዩቲዩብ ላይ የተገኘ ቪዲዮአቸውን ስመለከት ከማረኩኝ ንግግሮች አንዱ የጠ/ሚኒስትርነት ሥራቸውን ይወዱት እንደነበር የገለፁበት ነው (አብዛኛው እኮ የሚሰራው እንጀራ ሆኖበት ነው!) እናላችሁ … በትርፍ ጊዜያቸው ምን እንደሚሰሩ ተጠይቀው ሲመልሱ፤ “የተሰጠኝን ሥራ እወደዋለሁ፤ ኮንትራቴ ስምንት ሰዓት ነው፤ ነገር ግን ሥራውን ስለምወደው ከስምንት ሰዓት በላይ ነው የምሰራው፤ ስለዚህ ብዙ ትርፍ ጊዜ አለኝ ብዬ አልወስድም” ብለው ነበር፡፡ (የሚወደውን የሚሰራ እኮ የታደለ ነው!) አንዱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር የጠ/ሚኒስትሩን ንግግር ሰምተው ምን እንዳሉ ታውቃላችሁ? “እኔም የሳቸውን ሥራ እወደዋለሁ!” (ነውጠኛ አባባል እኮ ነው!)
እውነቱን ለመናገር ሰውየው የተዋጣላቸው ተናጋሪ ነበሩ፡፡ ተናግረው ሲያሳምኑ የሚያህላቸው አልነበረም፡፡ አላምንም ያለውን ደግሞ ቢያንስ በሳቅ ይሸኙታል (ባለማመኑ የታሰረ የለም!)
አንድ ጊዜ አገራቸው ላይ ኢንቨስት ሊያደርጉ የመጡ ዳያስፖራዎችን ሰብስበው ሲያነጋግሩ ብዙ ቅሬታና ወቀሳ ከቤቱ ተሰነዘረ - ወደ መለስ ወይም መንግስታቸው፡፡ በዚያ ላይ አብዛኛው ዳያስፖራ ከኢህአዴግ ጋር ሆድና ጀርባ ነው (በጥናት ሳይሆን ከምናየው ከምንሰማው!) እናም የያኔው መለስ ሁሉንም ከግምት ውስጥ አስገብተው ሲያበቁ፣ ለዳያስፖራው “ስሞተኞች” የሰጡት ምላሽ አዳራሹን በጭብጨባ አናጋው፡፡ ብልሃትና ብልጠት የተደባለቁበት የመለስ ንግግር የዳያስፖራውን ልብ እንደረታ መገመት አያዳግትም፡፡ እንዲህ ነበር ያሉት “ይሄ የእናንተ አገር ስለሆነ በቢሮክራሲው መልካም ፈቃድ ኢንቨስት የምታደርጉበት፣ የቢሮክራሲው መልካም ፈቃድ ሳይኖር ሲቀር ደግሞ አኩርፋችሁ የምትሄዱበት ሊሆን አይችልም፤ አማራጭ የላችሁም፤ አገራችሁ ነው፤ በእልፍ እስከመጨረሻው ድረስ መግፋት አለባችሁ፤ ማንም ሊያሰናክላችሁና ሊያስቆማችሁ አይገባም፡፡ እናንተን ከውጭ ኢንቨስተር የሚለየው ይሄ ነው፡፡ የውጭ ኢንቨስተር 190 ምናምን አገር አማራጭ አለው፤ እናንተ አማራጭ የላችሁም፤ አንድ አገር ብቻ ነው ያላችሁ …” እስቲ አስቡት … ይሄ ንግግር እንኳንስ ያለጠብ ያኮረፈ ዳያስፖራን ቀርቶ ደም ሊቃባ ያሰበን ባላጋራ እጅ አያሰጥም እንዴ? አንዳንዴ ሳስበው … አቶ መለስ ፓርቲያቸውን ኢህአዴግን ፈርተው እንጂ (ወይ አክብረው?) በዚህ ተናጋሪነታቸው የተቃዋሚ ጐራውን ሰብስበው ከጐናቸው ያሰልፉት ነበር፡፡ (በ97 ምርጫ ለቅንጅት ሊወዳደሩ ነው ተብሎ አልነበር?)
አንዱ የግል ሚዲያ ጋዜጠኛም ደሞዛቸው ስንት እንደሆነ ጠይቋቸው የሰጡት መልስም የሚያስገርም ነበር፡፡ “ደሞዜን በተመለከተ ፀረ-ሙስና የሁሉም ባለስልጣኖችን ደሞዝ አውጥቷል ይመስለኛል፤ ካላወጣ ግን እስከቅርብ ጊዜ ድረስ የነበረው 6400 ነው፤ የአሁኑ ጭማሪ ግን እኔ ጋ አልደረሰም፤ ሲደርስ የሚጨመር ነገር ካለ አሳውቃለሁ” እርግጠኛ ነኝ ብዙዎቻችን ይሄንን ንግግራቸውን አልተቀበልነውም፡፡ (ባይዋሹ እንኳ ያሾፉ ነው የመሰለን!) እሳቸው ካረፉ በኋላም ግን ባለቤታቸው ወ/ሮ አዜብ ያንኑ ደግመው ተናግረውታል፡፡ ክፋቱ ግን እሳቸውንም ሳንጠረጥራቸው አልቀረንም፡፡ እንዴ… ብናምናቸውማ ኖሮ የጠ/ሚኒስትር ደሞዝ ይሻሻል ብለን ሰልፍ እንወጣ ነበር፡፡ (የአገር ገፅ ግንባታ ያበላሻል እኮ!) እኔ የተቃዋሚ ፓርቲ ቢኖረኝ ኖሮ ይሄን ጥያቄ አንዱ የትግል አጀንዳዬ አደርገው ነበር (ከፀረ ሽብር ህጉ ቀጥሎ!)
እኔ የምለው ግን… አንዳንድ የመንግስት ባለስልጣናት እንዲህ ሙስና እላያቸው ላይ ያናጠጠው፣ “ደሞዝ እያነሳቸው ቢሆንስ?” ብላችሁ ታውቃላችሁ? (የመንግስት ባለስልጣናት እኮ የመላዕክ ስብስብ አይደሉም!)
ጋዜጠኛ መቼም ዕድል ካገኘ የማይጠይቀው ነገር የለውም (እንጀራው እኮ ነው!) አንዱ ጋዜጠኛ የጠ/ሚኒስትርነት ሥልጣናቸውን እንዴት እንደሚያዩት ጠይቋቸው እንዲህ አሉ “እንደ አመለካከቱ ነው … እንደምቾትም ማየት ይቻላል፤ እንደ እስር ቤትም ማየት ይቻላል” (አንዳንዱ ይሄኔ “ቃሊቲን አላዩ” ብሏቸው ይሆናል - በሆዱ!) “ለምሳሌ በትጥቅ ትግሉ ወቅት ከነበረው ሁኔታ ጋር ሳነፃፅረው የምቾት ነው … የቆሸሸ ልብስ አልለብስም፣ አልራብም፣ አልጠማም፣ በቂ መጠለያ አለኝ ወዘተ ወዘተ … ነገር ግን ከዚህ ሥራ ወጥቼ ሌላ አማራጭ ብፈልግ እራባለሁ የሚል ግምት የለኝም” በማለት ስለ ምቾቱ ገለፁ፡፡ በመቀጠል እስር ቤት የሚያሰኘውን ተናገሩ “በዚህ ሥራ ላይ በምትሆንበት ወቅት የመሰለህን መናገር፣ የመሰለህን ማድረግ አትችልም፡፡ አንድ ነገር ብል ምንድነው ትርጉሙ? በአገር ላይ ምን ጉዳት ያስከትላል? ድርጅቱ ላይስ … ምናምን የሚል መታሰብ አለበት … በሀገሪቱ በጣም ብዙ ችግሮች አሉ፤ የመጨረሻው ሃላፊነት ያንተ ነው፤ እነዚህን ነገሮች በምታስብበት ወቅት በተወሰነ ደረጃ እስር ቤትም ነው” እውነታቸውን እኮ ነው፤ ነፃነት ከሌለው ያው እስር ቤት ነው፡፡ (ተቃዋሚዎች ሰማችሁ አይደል!) በመጨረሻ ከመላው ኢህአዴግ እሳቸውን (መለስን) ብቻ የሚወድና የሚያደንቅ የተቃዋሚው ጐራ ደጋፊ ሰሞኑን ሹክ ያለኝን ሹክ ልበላችሁና ልሰናበት፡፡ “መለስ በህይወት ከነበሩበት ጊዜ ይልቅ ከሞቱ በኋላ በመንግስት ሚዲያዎች የበለጠ ሽፋን እንዳገኙ ታውቃለህ? … እኔ በደንብ ነው ያጠናሁት … ዳታ ሁሉ አለኝ … በስልጣን ላይ በቆዩባቸው 20 ዓመታት እንዲህ ትኩረት አልተሰጣቸውም”፤ ታፍነው ነበር እኮ!” አለኝ፡፡ (“እውነትም ጠ/ሚኒስትርነት እስር ቤት ነው!” አልኩ-ለራሴ)

 

ባለፈው ሀምሌ ወር በሳኡዲ አረቢያ በቤት ሰራተኛነት ተቀጥረው የሚሰሩ ሶስት ኢትዮጵያውያን በግድያ ወንጀልና የግድያ ሙከራ ፈፅመዋል በሚል ተወንጅለዋል፡፡
ይሄንን ተከትሎም አንድ የሳኡዲ ባለስልጣን፤ ኢትዮጵያውያን የቤት ሰራተኞች ወደ አገራቸው እንዳይመጡ መወሰኑን ተናግረዋል፡፡ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ለሥራ የሚጓዙ ኢትዮጵያውያን ከአገራቸው መንግስት የሚደረግላቸው ጥበቃና ከለላ ስለመኖሩ፣ በየአገራቱ የሚገኙ ኤምባሲዎችና ቆንስላ ፅ/ቤቶች በዚህ ረገድ ምን ተግባራትን እንደሚያከናውኑና የሳኡዲውን ጉዳይ በተመለከተ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ ከኢትዮጵያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ጋር አጭር ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡

በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት በችግር ላይ ለሚገኙ ኢትዮጵያውያን ምን እየተደረገ ነው?
በህገ ወጥ መንገድ የሚሄዱት ላይ የእውቀት ችግር አለ፡፡ የሚሄዱበትን አገር ቋንቋ፣ ስነልቦና፣ በአጠቃላይ ያለውን ነገር ሳያውቁ የሚሄዱ ይበዛሉ፡፡ በስደት ላይ ያሉ ዜጎችን የማስመለስ ስራ እየተሰራ ነው፡፡ ቢሆንም ማነቆዎች አሉ፡፡ ስራው እየተሰራ ያለው በተለያዩ ሀይሎች ነው፡፡ ፖሊስ፣ ኢሚግሬሽን፣ ዓለምአቀፍ የስደተኞች ጉዳይ ድርጅት (አይኦኤም) ፣ ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ፣ ሰራተኛና ማህበራዊ፣ በውጪ ያሉ የኢትዮጵያ ቆንስላ ፅህፈት ቤቶችና ሌሎችም በየፊናቸው ይሰራሉ፡፡ ችግሩ ግን እጅግ የተወሳሰበ ነው፡፡
ወደ መካከለኛው ምስራቅ በህገወጥና በህጋዊ መንገድ በሚሄዱት መካከል ያለው ልዩነት የአካሄድ ነው እንጂ የሚገጥማቸው ችግር ተመሳሳይ ነው ይባላል...
ትክክል ነው፡፡ በህገወጥ ተሄደ በህጋዊ መንገድ ችግሩ ተመሳሳይ ነው፡፡ በሚሄዱበት አገር ማህበራዊ ዋስትና አላቸው ወይ? የጤና ኢንሹራንስ እና ሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮችም ምላሽ ይፈልጋሉ፡፡ ችግር ሲደርስባቸው የሚያመለክቱበት መንገድ አለ ወይ? ወደ አገራቸው መመለስ ቢፈልጉ መመለስ የሚችሉበት መንገድ አለ? ወዘተ-- የሚሉት መፈተሽ አለባቸው፡፡ ከሌሎቸ የእስያ አገራት ለተመሳሳይ ስራ ወደ አረብ አገራት የሚሄዱ ሰዎቸ ለሚሰማሩበት ሥራ ስራ ስልጠና ይወስዳሉ፡፡ በኛ በኩል ይህ የለም፡፡ በህጋዊ መንገድ ቢኬድም የሚሰራው ስራ ህጋዊ ነው ወይ የሚለው አጠያያቂ ነው፡፡ የሚጠብቃቸው አቀባበልም መታየት አለበት፡፡
ኢትዮጵያ በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት በቂ እና የተሟሉ ኤምባሲዎች አላት ማለት ይቻላል?
በውጪ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የሚሰራው ስራ አደጋ ከደረሰ በኋላ እሳት የማጥፋት ሰራ ነው፡፡ በመካከለኛው ምስራቅ ኤምባሲዎች ያሉን በተወሰኑ ቦታዎች ነው፡፡ የሰው ሀይል እና የገንዘብ ብቃታቸው ከችግሩ ጋር ተመጣጣኝ ነው ወይ የሚለው እየታየ ነው፡፡ በአንዳንድ አካባቢዎች ብዙ ኢትዮጵያውያን በመጠለያ ውስጥ ናቸው፡፡ እነዚህን ዜጎች ተመላልሶ መጠየቅ፣ ፍርድቤት ጉዳይ ያለባቸውን የህግ ድጋፍ መስጠት፣ የካሳ ጥያቄ ለሚያነሱ የህግ ምክር መስጠት የመሳሰሉትን በዝርዝር አይቶ የማስፈፀም አቅም ላይ ችግር አለ፡፡
ኤምባሲዎቹ ወይም ቆንስላ ፅህፈት ቤቶቹ በመካከለኛው ምሥራቅ ተቀጥረው የሚሰሩ ኢትዮጵያውያንን ያውቋቸዋል?
ከአገር ቤት ከወጡ በኋላ በኤምባሲዎቹ የመመዝገብ ባህል በጣም አነስተኛ ነው፡፡ መመዝገብ እንዳለባቸው ግን መረጃ አላቸው፡፡ በህጋዊ መንገድ የሚጓዙትም በሰራተኛና ማህበራዊ ሚኒስቴር በኩል ተዋውለው ቪዛቸውን ካገኙ በኋላ ይሄዳሉ እንጂ ኤምባሲዎቹና ቆንስላ ፅህፈት ቤቶቹ መረጃ የላቸውም፡፡ ከሰራተኛና ማህበራዊ ሚኒስቴር ጋር ያለው ቅንጅትም እጅግ የላላ ነው፡፡ አሁን እየተጀመሩ ያሉ ስራዎች አሉ፡፡ ነገር ግን ከችግሩ ስፋት ጋር ሲነፃፀር በቂ አይደለም፡፡ ሌላው ከዚህ በቤት ሰራተኛነት የሚሄዱት እንኳንስ ከኤምባሲ ጋር ሊገናኙ ከማህበረሰባቸው ጋር እንኳን እንዲገናኙ አይፈቀድላቸውም፡፡ በተቀባይ አገሮች በኩል ሰራተኞቹ እንዲህ አይነት ግንኙነት እንዲፈጥሩ አይበረታቱም፡፡ በአካል አግኝቶ ችግራቸውን ለማወቅ ይቅርና በስልክም ማግኘት አስቸጋሪ ነው፡፡
ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ይህን ችግር ለመፍታት ምንድነው የሚያደርገው ?
እንግዲህ ከላይ የተጠቀሱት ችግሮችና የተቀባይ አገሮች ህግ ተደምረው ለጉዳዩ አፈጣኝ እልባት እንዳይሰጠው አስተዋፅኦ ያደርጋሉ፡፡ በውጪ ጉዳይ ሚሲዮኖች ወደ እዚህ የሚገባው ቅድም እንዳልኩት አደጋ ከደረሰ በኋላ ነው፡፡ የችግሩ ትልቁ ምንጭ ያለው አገር ቤት ነው፡፡ ትልቁ መፍትሄ መሰጠት ያለበት አገር ቤት ነው፡፡ የሚሄዱት ወገኖች አውቀውና ሰልጥነው እንዲሄዱ ማድረግ፤ ወደዚያ እንዳይሄዱ ስራን መፍጠር እና መልካም አስተዳደርን ማጠናከር ያስፈልጋል፡፡
የሰሞኑ የሳኡዲ ሁኔታስ እንዴት ይታያል?
የህገወጥ ዝውውር ምንጭ፣ መተላለፊያና ተቀባይ አገሮች አሉ፡፡ እዚህ ላይ ሶስቱም ወገኖች ተቀራርበው መስራት አለባቸው፡፡ የውጪ ጉዳይ አንዱ ድርሻም ይሄ ነው፡፡ የሳኡዲውን ሁኔታ በተመለከተ እንደዚህ ዓይነቶቹ ውንጀላዎች በየጊዜው ይቀርባሉ፡፡
ሰሞኑን ግን ጨምረዋል፡፡ እንዲያውም አንድ የአገሪቱ ባለስልጣን የቤት ሰራተኞች ከኢትዮጵያ መምጣት የለባቸውም ብለዋል---
ይህን ውንጀላ ማጣራቱ አስቸጋሪ ቢሆንም በጥቅሉ እነዚህ ሰዎች የሚሰሩት ስራ እጅግ አስከፊ ነው፡፡ የስሜት መናወጥ አለ፡፡ አንዳንዴ የተሰጣቸውን ስራም አያውቁትም፡፡ ዘመናዊ እና የረቀቁ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ለመጠቀም ልምዱ የላቸውም፡፡ በዚህ ምክንያት በራሳቸው እና በተቀጠሩበት ቤት የቤተሰብ አባላት ላይ ጉዳት ሊያደርሱ ይችላሉ፡፡
በሀምሌ ወር ብቻ ሶስት ኢትዮጵያውያን የቤት ሰራተኞች የግድያ እና የግድያ ሙከራ አድርገዋል በሚል ተወንጅለዋል፡፡ በውጪ ጉዳይ በኩል ምን እየተደረገ ነው?
ውጪ ጉዳይ ዜጎችን መታደግ በሚል ማእቀፉ፣ የህግ የምክር አገልግሎት የሚሰጥበት፤ ጉዳያቸው ፍርድ ቤት ከቀረበ በትክክል ሊዳኝ የሚችልበትን ሁኔታ መከታተል፣ ጠበቃ ቀጥሮ መሟገት እንዳለበት ያስቀምጣል፡፡ ለዚህ ሁሉ አቅም አለ ወይ? ከተባለ የለም ፤ እጥረት አለ። ነገር ግን ተቋሙ ግዴታ አለበት፡፡ አንዳንድ ሚሲዮኖች ያደርጋሉ፤ አንዳንዶች አያደርጉም፡፡ ለምሳሌ በፑንትላንድ የሰው ህይወት አጥፍቶ የነበረን ኢትዮጵያዊ ጉዳይ ሚሲዮናችን ከአገሪቱ መንግስት ጋር ባደረገው ውይይት የተጠየቀውን ካሳ አንድ ግለሰብ ከፍሎለት ነፃ ወጥቷል፡፡
በቅርቡ ከሳኡዲ የተሰማው “ልጅ ገደለች፤ በሻተር አነቀች” የሚለው ውንጀላ የት እንደደረሰ ባላውቅም፤ ሰሞኑን በመካከለኛው ምስራቅ የሚገኙ የኛ ሚሲዮን ሀላፊዎች አዲስ አበባ ስብሰባ አድርገዋል፡፡ ምን ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው በስፋት ተወያይተዋል፡፡ ደካማ የቆንስላ እንቅስቃሴ ባለባቸው ፅህፈት ቤቶች ላይ ጠንከር ያለ ዜጎችን የመደገፍ ስራ እንዲሰራ አስፈላጊውን የሰው ሀይል ማሟላት እና የገንዘብ አቅምን ማጠናከር፤ ከአገሩ መንግስት ጋር እንደ አስፈላጊነቱ በጉዳዩ ላይ መወያየት እና በየአካባቢው ከሚገኙ የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ጋር መወያያት የሚሉት በመፍትሄ ተቀምጠዋል፡፡ አንዳንድ አካባቢዎች አስከሬን መጫኛ እንኳን የሚጠፋበት አጋጣሚ አለ፡፡ ለዚህ ደግሞ ከመንግስት የተመደበ በጀት የለም፡፡
የኢትዮጵያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር በተለይ ከመካካለኛው ምስራቅ አገሮች ጋር በተያያዘ ለዜጎች ግድ የለውም፤ የሳኡዲን የስራ ስምምነት የወሰደው አንዳንድ አገሮች በዜጎቻቸው ላይ በሚደርሰው እንግልት ሳቢያ ስምምነቱን በማቋረጣቸው እንደሆነ ይነገራል፡፡ በዚህ ላይ የመስሪያ ቤቱ ምላሽ ምንድን ነው?
ከመካካለኛው ምስራቅ አገሮች ጋር ያለን ስምምነት የሌበር ስምምነት ነው፡፡ እስከአሁን ሲሰራበት የነበረው አሰራር ለሁለቱም ወገኖች ከሚሰጠው ጥቅም አንፃር ታይቶ ነው፡፡ እነሱ ሰራተኛ ይፈልጋሉ፤ እኛ ደግሞ ሰራተኛ አመንጪ አገር ነን፡፡ የሳኡዲንም የተፈራረምነው በአለም አቀፍ ህጎች እና በሌሎቸ ተዛማጅ ህጎች መብታቸው እንዲጠበቅ ይደረጋል በሚል ነው፡፡
በመንግስት በኩል የስራ ጉዞውን ለማስቆም እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው የሚባለው እውነት ነው?
መንግስት ገብቶበት ስርአት ማስያዙ ተገቢ ነው፡፡ ለስራ የሚደረግ ዝውውር ግን አለም አቀፍ ክስተት ነው፡፡ መንግስት ያንን ማስቆም አይችልም፡፡ ለዜጎች ጥበቃ ሲባል ለጉዞ የተዘጉ አንዳንድ አገራት ግን አሉ፡፡
የሳኡዲንስ ጉዳይ በተመለከተ?
በቅርቡ የሳኡዲ መንግስት አወጣው ከተባለውና ከላይ ከተጠቀሰው ውጪ ሁለታችን ቁጭ ብለን አልተነጋገርንም፡፡ ቀጣዩን መከታተል ነው የሚሻለው፡፡

Published in ህብረተሰብ

       ሰሞኑን፣ ወደ ዝግጅት ክፍላችን አንድ በእድሜ ብዛት ንትብ ያለ ባለ 34 ገጽ መጽሔት መጣልን። ክፍለሀገር ከሚኖር፣ የእነ ፈቃደ አዘዘ የቀድሞ ተማሪ እጅ ከ40 ዓመት በላይ የቆየው ‹‹ቴዎድሮስ›› የተሰኘው ይኽ መጽሔት፣ ደብረታቦሩ ከተማ በሚገኘው፣‹‹ዳግማዊ ቴዎድሮስ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት›› በ1964 ዓ.ም. በሰቴንስል ተባዝቶ እንደተሰራጨ ታውቋል፡፡
በወቅቱ፣ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ለአንድ ዓመት የማስተማር አገልግሎት የመስጠት ግዴታ ስለነበረባቸው፣ የያኔዬው የ22 ዓመቱ ትንታግ ወጣትፈቃደ አዘዘና ሌሎች 6 ጓደኞቹ፣ በዳግማዊ ቴዎድሮስ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት የማስተማር ‹‹ሰርቪስ›› ይወጡ ዘንድ፣ የዛሬው የደቡብ ጎንደር መስተዳድር ዞን ዋና ከተማ በሆነው ደብረታቦር፣ ከትመው ነበረ፡፡ እናም፣ መጽሔቱ፣ በዚያ የአንድ ዓመት የማስተማር ቆይታቸው ወቅት ያዘጋጁት ሲሆን፣ በአማርኛና በእንግሊዝኛ የቀረቡ መጣጥፎች፣ ዜናዎች፣ ለፈገግታ ያህሎች፣ የአካባቢ ገለጻዎች፣ ግጥሞች፣ የካርቱ ሥዕሎች ወዘተ. ቀርበውበታል፡፡
ታዲያ በመፅሄቱ ላይ በንባብ ከቀረቡ ፅሁፎች መካከል፣በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ማስተማርና መመራመር ከጀመሩ፣ ዘንድሮ 40ኛ ዓመታቸውን የደፈኑት የዶ/ር ፈቃደ አዘዘ ፅሁፎችም ይገኙበታል። “ድር ቢያብር አንበሳ ያስር” በሚል ርዕስ ያቀረቡት መጣጥፍ፣ በወቅቱ በተማሪዎች ንቅናቄ ሲስተጋባ የነበረው የብሄር/የጎሳ ፖለቲካ የደረሰበት ጫፍና የወደፊት ጦስ አቀንቅኗል፡፡ “ታዲያኮ ኢትዮጵያዊ ነኝ ማለት ቀርቶ ‹አጅባሬ ነኝ!›፣ ‹ካሳንችሴ ነኝ!› ወዘተ. ማለት ሊመጣ ነው፡፡ በአባትና ልጅ መሀከል ልዩነት አይፈጠር ብላችሁ ነው? ወይስ ተፈጥሯል? የሚለውን ገለፃ ከዛሬ ነባረ ሁኔታ ጋር በንፅፅር ስናየው የትንቢት ቃልም ይመስላል፡፡
“መቼ ሆን?” በሚል ጥያቄያዊ ርዕስ ለዘብ ብለው የቀረቡ የአስተውሎት ምልከታዎች ፣ስለ ደብረታቦር ከተማና ህዝብ ማህበረ ባህላዊና ኢኮኖሚያዎ ሁኔታ ይጠቁማሉ፡፡ የምልከታዎቹ ዋጋ ግን፣የትናንሽ የገጠር ከተሞችን ጭምር ማህበረ ባህላዊ የኑሮ መልኮች፣የሰው ሰራሽና የተፈጥሮ ክስተቶችን ወዘተ በወቅቱ የመዘገብን አስፈላጊነት ከማመልከታቸውና ከማንቃታቸው ጭምር ሊመዘዝ ይችላል፡፡ ዛሬ ላይ የደብረታቦር ከተማና ህዝብ የለውጥ ሁኔታን ቃኝቶ ምልከታውን ለሚያከፈለን ፀሐፊም መልካም አጋጣሚ ነው እንላለን፡፡ ለማንኛውም ከመፅሄቱ እንደወረደ የቀረቡትን ፁሁፎች እንደሚከተለው አቅርበናል፤

ድር ቢያብር አንበሳ ያስር
በማንኛውም ህብረተሰብ ውስጥ አንድ ሰው ብቻውን ኢምንት ነው፡፡ ሀይል የለውም፡፡ ስርዓት አይኖረውም፡፡ አላማውም ግላዊ ነው፡፡ ብቻውን ከመቶ ኪሎ ጤፍ እንደ አንዲቱ የጤፍ ቅንጣት ነው። ጤፍ ብቻዋን አታጠግብም፡፡ ሰውም ብቻውን ዋጋ የለውም፡፡ ከሰው ከተባበረ ግን እራሱን ሊያሻሽልና ሊጠብቅ፣ ባላንጋራውን ሊያጠቃ ይችላል፡፡ ሥራውም እንደ አንዷ ጤፍ ሳይሆን እንደምንበላው እንጀራ አንጀት አርስ ይሆናል፡፡
ታድያ ምነው የሰው ልጆች ልብ ተራራቀ? ምነው ተከፋፈለ? ምነው ሕብረትን ጠላ? ለምንስ በጠቅላላው በሰው ልጅ ወንድማማችነት እንደመመስረት የጎሳ ዝምድና ይመሰረታል? ለምን ወገን ይለያል? ሀገር የጋራ ነው ተብሏል፡፡ ታዲያኮ ዝምድናውም የጋራ ነው ማለት ነው፡፡ ፍቅሩ የሁሉ ነው ማለት ነው፡፡ ነገር ግን አሁን የሚታየው ድርጊት ህሊናን የማያስደስትና አንጎልን የሚያናውጥ ነው፡፡
ጠለቅ ብለን ስንመለከት ብዙ ጅል ነገር እናገኛለን፡፡ አማራና ትግሬ ወገን መርጦ፣ ና ጉራጌ ተከፋፍሎ፣ ጋምቤላና ኩናማው ተለያይቶ ደም እንዳየች ውሻ በተገናኘ ቁጥር (‹‹ሲጣላ››) ሥራው እንዴት ይሠራ? እንዴት ለትምህርት እናስብ? እንዴት ለአንዲቷ ለመከረኛዪቱ እናት እናስብላት? ልባችን ለየብቻ ሆነ፡፡ ሥራችን ለየብቻ ሆነ፡፡ በመሀከል ግን ተጎዳን፡፡ እሷንም እንደማቀቀች ጎባጣ አሮጊት፣ ቀንታ (ቀና ብላ) ዓለሟን እንዳታይ ዓይኗን አጠፋነው፡፡
የሚገርመው ደግሞ ይህ ብቻ አይደለም፡፡ ይህ ልዩነቱ እየጠበበ ነው የሚሄደው፡፡ አማራው እንደገና ጋይንት፣ ቡልጋ፣ እስቴ፣ ደብረማርቆስ ወዘተ. እያለ ወገን ይለያል፡፡ ጋላውም አሩሲ፣ ሰላሌ፣ በቾና ወለጋ ወዘተ. እያለ ይከፋፈላል፡፡ ትገሬውም እንደዛው፡፡ ሌላውም እንደዛው፡፡ ካፍንጫችን እርቀን ስናስብ ደግሞ ቀስ እያለ በትውልድ መንደር የሚደረግ ልዩነት ሊመጣ ሞቆብቆቡን እንረዳለን፡፡ የአጅባርና የአስፋው ግራር፣ የአራት ኪሎና የስድስት ኪሎ ወዘተ. ልጆችስ እየተፈላለጉ ይጣሉ የለ? ታዲያኮ ኢትዮጵያዊ ነኝ ማለት ቀርቶ ‹‹አጅባሬ ነኝ!››፣ ‹‹ካሳንችሴ ነኝ!›› ወዘተ. ማለት ሊመጣ ነው፡፡ በአባትና ልጅ መሀከል ልዩነት አይፈጠር ብላችሁ ነው? ወይስ ተፈጥሯል?
ይህ ሁሉ የሚመጣው የስልጣኔን ጮራ፣ የትምህርትን ውጋገን ካለማገኘትና ከዚህም በላይ እውነተኛ የሀገር ፍቅር ከማጣት ነው፡፡ ስለዚህ ያገሬ ሰው ስማኝ፣ ተባበር፡፡ አትበታተን፡፡ ጠላትህን አታስደስት፡፡ ከተባበርክ እንኳን ረሃብን፣ ድንቁርናን እና ሌሎች ልዩ ልዩ በሽታዎችን ማጥፋት ትችላለህ፡፡
ተራራውን ብትገፋው ይገፋልሃል፡፡ ወደመሬት ማውረድ ወደሰማይ ማውጣት፣ ማስጠምም ማዳንም ያንተው ይሆናሉ፡፡ አትፍራ ሁሉም የሚፈልግ ህብረት ነው፡፡ አንድነትህን የሚጠላ የለም፡፡ ልብህን ይክፈተው፡፡ ብርታቱን ይስጥህ፡፡
ፈቃደ አዘዘ
የሰርቪስ መምህር
(በግል ምክንያት ሆሄ አልተጠበቀም)
መቼ ይሆን?
የደብረ ታቦር ሕዝብ መኪና በበጋ ሲመጣ በእልልታ መቀበሉ የሚቀረው?
ደብረ ታቦር መብራትና መንገድ ውሃና በቂ የሕክምና ጣቢያ የሚኖራት?
አንድ ብልህ ነጋዴ በላመነት የሚሰሩ ቦርሳዎችና ሻንጣዎች ኢንዱስትሪ የሚያያቋቁመው?
የደብረ ታቦር ጠላና ጠጅ የሚበላሸው?
የሚሲዎን ሀኪም ቤት አዋቂ ዶክቶሮች አስመጥቶ ሀብታም ደኃ ሳይል በትክክል የሚያክመው?
የደብረ ታቦር የ‹‹ቴዎድሮስ›› ቡድን (የእግር ኳስ) የቤጌምድር አሸናፊ (ሻምፒዎን) ሆኖ አዲስ አበባ የሚመጣው?
ፍርድ ቤት የሚመላለሰው ተሟጋች ቁጥር የሚቀንሰው?
እማማ የኔ ገላ የሚወፍሩት?!!!!!!!!
ተማሪዎችና መምህራን በጓድ ተከፋፍለው በትርፍ ጊዜያቸው ሕዝቡን በየቤቱ ሄደው የሚያስተምሩት?
የበኣል ቀናት ተቀንሰው የሥራ ቀናት የሚጨመሩት?
‹‹ፋርጣ ብር ቢያጣ ነገር አያጣ›› የሚባለው አነጋገር ዋጋ የሚያጣ?
በየመንገዱ፣ በየሜዳው፣ በየአጥር ጥጉና በየዱሩ መጸዳዳት የሚቀረው?
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በጭነት መጫኛ አውሮፕላን ሰው ማመላለሱን የሚተወው?
የደብረ ታቦር ተማሪዎች ለኮርስ መስገብገባቸውን ትተው በትምህርታቸው ለመግፋት የሚያስቡት?
አዝማሪዎች በቀን በቀን ብር አምጡ ማለት የሚተዉት?
የሰርቪስ መምህር - ፈቃደ አዘዘ
1964፣ ደብረ ታቦር

 

Published in ህብረተሰብ

         ገና ከእንቅልፋችን ስንነቃ “ሰላም አውለኝ” ብለን በየእምነታችን መጸለይ የተለመደ ነው፡፡ ግን ጸሎታችን ከፈጣሪ ዘንድ አለመድረሱ ወይም ደርሶ ተቀባይነት በማጣቱ፤ ብቻ በሆነ ምክንያት ልመናችን አይሰምርም፡፡ “ሰላም አውለኝ” ብለን ወጥተን በንዝንዝና በንትርክ ቀኑ ያልፋል፡፡
ብስጭቱ የሚጀምረው ልክ ከቤታችን እንደወጣን ነው፡፡ ታክሲ ለመጠበቅ ረጅም ሰልፍ ውስጥ መቀላቀል አለብን፡፡ ሰልፍ መያዙ ከኪስ መንታፊዎች የሚታደግና የስልጣኔ ምልክት ቢሆንም ጭቃና ዝናብ በበዙበት ቦታ ብዙ መቆም ያበሳጫል። ከእልህ አስጨራሽ ሰልፍ በኋላ የተጠበቀው ታክሲ መጥቶ ገብተን ወንበር ስንይዝ ደግሞ ሌላ የሚያበሳጭ ጉዳይ ይጠብቀናል፡፡

ታክሲው ያረጀ/አብዛኞቹ ታክሲዎች ያረጁ ናቸው/ይሆንና ጣራው ሊያፈስ ይችላል፡፡ ታክሲ ውስጥ ደግሞ ጥላ መዘርጋት አይቻልም፤ እናም ብስጭቱ ይቀጥላል፡፡ ወይም በወላለቁ የታክሲው ወንበር ብረቶች ልብሳችን ይቦደስና ሌላ ብስጭት ውስጥ እንገባለን፡፡
ለነገሩ ታክሲው መገኘቱም እንደ ምረቃ ሊታይ የሚችል ነው፡፡ ምክንያቱም ከዚያ ሁሉ ሰልፍና ጣጣ በኋላ ሥራ ቦታ ሲደረስ ሌላ ብስጭት ይጠብቃልና ነው፡፡ ትንሽ ሰዓት ካለፈ መንግሥት በይፋ ሁለት ሁለት መኪኖችን ለግላቸው የመደበላቸው አለቆች በትር የዋዛ አይሆንም፤ አንድም ደሞዝን ይቆርጣሉ፤ ወይም “ተነሳሽነት ጐድሎታል፤ ፀረ ልማትና ፀረ ትራንስፎርሜሽን ነው” ብለው ከሥራ ሊያፈናቅሉ ይችላሉ፡፡ እነሱና ቤተሰቦቻቸው ግን ከህዝብ በተሰበሰበ ገንዘብ በውድ ዋጋ በተገዙ ዘመናዊ አውቶሞቢሎች ይንፈላሰሳሉ፡፡
ለምንዝሩ ህዝብ ግን “ተሟሙቶ” በጊዜ ከሥራ ቦታ መድረስ ግድ ይሆናል፡፡ በታክሲ ወረፋ፣ በዝናብና በጭቃ መከራውን አይቶ ሥራ ሲገባም ምቹ የሥራ ሁኔታ አይጠብቀውም፡፡ አለቆች ለራሳቸው ምቾት እንጂ ለሥራውና ሠራተኛው እምብዛም ትኩረት ስለሌላቸው የሚጐዳው ያው የፈረደበት ምንዝሩ ይሆናል፡፡ “ልሥራ” ብሎ ሲነሳ ወይ ኮምፒውተር የለም፤ ወይም ወረቀትና እስክብሪቶ አይኖርም፡፡ እንዲሰጠው ሲጠይቅም ጐታታ መልስ እየተሰጠው ጊዜውን በከንቱ ያባክናል፡፡ ግን ደግሞ በተወሰነ ጊዜ ውስጥ ሥራውን አጠናቅቆ እንዲያቀርብ ግዴታ ይጣልበታል፤ በዚህም ሲበሳጭ ይውላል፡፡
ግማሹን ቀን በዚህ ዓይነት ፍሬ አልባ ሁኔታ ያሳልፍና ምሳውን ሊቀምስ በተቋማት ክበቦች አሰሳውን ይቀጥላል፡፡ እዚያም ሌላ ብስጭት ይጠብቀዋል፡፡ ከእሱ የባሱ ምስኪን አስተናጋጆች “የመ/ቤቱ ሠራተኛ ለመሆንህ ቅድሚያ መታወቂያህን አሳይ” ሊሉት ይችላሉ፡፡ ርቦትና በሁኔታዎች አለመሟላት ሲበሳጭ ውሎ ምግብ ፍለጋ ለመጣ ሰው ሌላ ንዝንዝ መፍጠር ስሜትን በእጅጉ ይጐዳል፡፡
ውጣ ውረዱን አልፎ ምግብ ቢቀርብለትም እዚህ ግባ የማይባል መናኛ ይሆንበትና እንደነገሩ ቀማምሶ ዋጋ ሲጠይቅ በሚነገረው የገንዘብ መጠን ይደነግጣል፤ መደንገጥ ብቻ ሳይሆን በአያሌው ይበሳጫል፡፡ የሚያበሳጨው የዋጋው መናር ብቻ ሳይሆን የአቅርቦቱ አለመመጣጠን ነው፡፡ እንጀራው ነፋስ ሽው ቢል ይዞት ሊሄድ የሚችል፤ ወጡም ከእህል የተሰራ የማይመስል ዝባዝንኬ ሲሆንበት ለገንዘቡ ብቻ ሳይሆን ለጤናውም ጭምር በመስጋት ይበሳጫል፡፡
ዋጋው የተወደደበትን ምክንያት ሲያጤን ከጥሬ ዕቃ መወደድ ጋር ተዳምሮ በተጨማሪ ዕሴት ታክስ ሰበብ መሆኑን ይገነዘብና እንደገና ይበሳጫል፤ ከደሞዙ ላይ ለሥራ ግብር 35 በመቶ፣ ከሚመገበውና ከሚጠጣው ሻይ ላይ 15 በመቶ፤ በአጠቃላይ የደሞዙ ሃምሳ በመቶ ለመንግሥት ገቢ እንደሚደረግ ሲገባው ብስጭቱ ይጨምራል፡፡ በህገወጥ መንገድ የሚነግዱና ህጋዊ ሆነውም ለመንግሥት የሚያስገቡትን ገቢ (ግብር) ከራሱ ጋር ሲያነፃፅረው እንደገና ሊበሳጭ ይችላል፤ ህገወጥነትንም ያልማል፡፡
ከ “ምሳ” መልስ ወደ ሥራው ሲመለስም ያው የተለመደው ምቹ ያልሆነ የሥራ ሁኔታ ይጠብቀዋል፡፡ እንደምንም ተፍጨርጭሮ የዕለቱን ተግባር በመከወን ለአለቃው ሲያቀርብም “ጥራቱን አልጠበቀም” ተብሎ ይወረወርለታል፤ ምክንያቱን ግን አይጠየቅም፡፡ የሥልጠና ዕድል ሲገኝም “አቅም የለውም” ለተባለው ሳይሆን ከአለቃ ጋር ለሚሞዳሞዱ ቅድሚያ ይሰጣል፡፡ በአፈጻጸም ድክመት ግን ቀድሞ ይወቀሳል፤ በዚህም ይበሳጫል።
የዕለቱ የሥራ ሰዓት በዚህ መልኩ ይገባደድና ወደ ቤቱ ለመሄድ የተለመደውን የታክሲ ወረፋ ይይዛል፤ በዚህ ጊዜ ከጥዋቱ የተለየ መስተንግዶ ይጠብቀዋል፡፡ ለሁለት ሰዎች በተዘጋጀው ወንበር ላይ ሶስትና አራት ሰዎች እንዲቀመጡ ግድ ይባላሉ፡፡ በተለይ እንደ አጋጣሚ ወፋፍራም ሰዎች ጐን ለጐን ከተቀመጡ ያለው ጣጣ በቀላሉ የሚገለጽ አይሆንም፡፡ ከቦታው ጥበት በላይ ከጐኑ የሚቀመጡት ሰዎች ወይ ድብን አርገው የጠጡ፣ አለዚያም ንጽህናቸው የተጓደለ ይሆንና እንደ ኦሪታዊው ኢዮብ በመፈጠሩ ሊያዝን ይችላል፡፡
ከዚህ ሌላ ባለ ታክሲው ከመጠን በላይ ትርፍ ሰው በመጫኑ ከትራፊክ ፖሊስ ለመሰወር ሲል በአልባሌ መንገድ መጓዝ ይጀምራል፤ “ለምን በተገቢው መንገድ አትጓዝም” ብሎ የሚጠይቅም የለም፡፡ የሚጠይቁ አንዳንድ ሰዎች ቢኖሩም ወያላው ክብራቸውን ከፍና ዝቅ አርጐ ያዋርዳቸዋል፡፡
የከተማው የትራንስፖርት መ/ቤት በወሰነው መንገድ ሳይሆን የታክሲ ወያላና ሹፌር በመረጡት “አቋራጭ” መንገድ መጓዝ ሌላው የብስጭት መነሻ ነው፡፡ ታክሲ አሽከርካሪዎች አቋራጩን መንገድ የሚመርጡት ትርፍ ሰው በመጫን በአቋራጭ ለመክበር አስበው ነው፡፡ በመደበኛው መንገድ ቢጓዙ የትራፊክ ፖሊሶች ሊይዟቸው ይችላሉ። ስለዚህ ትራንስፖርት መ/ቤቱ በወሰነው ሳይሆን ለእነሱ ህገወጥ አሠራር በሚያመች አቋራጭ መንገድ ሰውን ያለፍላጐቱ እየወሰዱ ህገወጥ ክፍያ ይጠይቁታል፡፡
በዚህ ዓይነቱ ውስብስብ ውሎ ቀኑን የገፋ ሰው በጊዜ ከደሳሳ ጐጆው ገብቶ ማረፍ ቢፈልግም ከቤቱም ብስጭት ቀድሞ ይጠብቀዋል፡፡ ገና ከቤቱ በር ሲደርስ መብራቱ ሁሉ ድርግምግም ብሎ ወንበዴ የወረረው ሰፈር መስሎ ይጠብቀዋል፤ የረባ ምሳ ባለመብላቱ ሲበሳጭ ውሎ ከቤቱ ሲደርስም ያገኘውን አብስሎ እንዳይቀምስ ሁኔታዎች ይዘጋጉበታል፡፡
በመጣበት እግሩ ተመልሶ በመሄድ እንጀራ ለመግዛት በየሱቁ ይንከራተትና የሚያገኘው እንጀራም ያው ነፋስ ሊወስደው የሚችል ሆኖበት ይበሳጫል፡፡ የሚያበሳጨው የእንጀራው መሳሳት ብቻ ሳይሆን ዋጋውም ጭምር ነው፡፡ ድሮ አንድ ክትፎ ይበላበት በነበረው ዋጋ አንድ ስሙ ብቻ እንጀራ የሆነ ነገር ሲገዛ በእርግጥም ቢናደድ የሚያስፈርድ አይሆንም፡፡
ሰውየው ላጤ ከሆነ ይህም ላያስደንቅ ይችላል። ትዳርና ልጆች ካሉት ግን ጣጣውና ኃላፊነቱ እጅግ ከባድ ይሆናል፡፡ እንጀራ ብቻ ሳይሆን ሻማ መግዛትም ግድ ነው፤ የሻማው ዋጋም ድሮ አንድ ወደል ወሰራ ዶሮ ይገዛበት የነበረው መሆኑን ሲያውቅ ብስጭቱ ይጨምራል፡፡
ይህን ሁሉ ከውኖ እንደገና ወደቤቱ ሲመለስም ሌላ ጣጣ አይኑን አፍጥጦ ይጠብቀዋል፡፡ ልክ እንደመብራቱ ውሃውም “የውሃ ሽታ” ይሆንበታል። በሐምሌና ነሐሴ ውሃ ማጣት ማለት አስገራሚም አሳዛኝም ጉዳይ ነው፡፡
መብራቱ “ ወደ ሱዳንና ጅቡቲ ተልኮ ነው” ይባላል፤ ግን ውሃው ደግሞ ወዴት ተልኮ ይሆን ማለቱ አይቀሬ ነው፡፡
“የታህሳስን ራብ የሐምሌን ውሃ ጥም እናት አታውቀውም” የሚባለውን ብሂል መገንዘብ የሚያሻው እንዲህ ዓይነት ግራ አጋቢ ገጠመኞች ሲኖሩ ይመስለኛል፡፡ መብራት ከጠፋ የነዳጅና የማገዶ አቅርቦት ሊኖር ይገባል፤ እሱም ከዘመኑ ኑሮ ጋር ሊሄድ አይችልም፡፡ ብዙ ቤቶች ወደ ፎቅነት እየተቀየሩ ናቸው፡፡ ፎቅ ላይ ደግሞ እሳት ማንደድም ሆነ ከሰል ማቀጣጠል አይመችም፤ ተገቢም አይደለም፡፡ ለዚህም ነው ከሚያስደስቱ ጉዳዮች ይልቅ የሚያበሳጩት የሚያይሉት፡፡
እናም ሀገራችን፤ በተለይም ከተማችን በብስጭት ውለን፣ በብስጭት ተጉዘን፣ በብስጭት የምናድርባት፤ በአጠቃላይም የብስጭት ፋብሪካዎች የተገነቡባትና ብስጭት ይመረትባት ይመስል የብስጭት ጐተራዋ አድርጋናለች፡፡ ደስታችን ከውስጣችን ሙጥጥ ብሎ ወጥቶ የገባበት ጐሬ ጠፍቶናል፡፡
ይህ ሁሉ ጣጣ መድረሻ ሲያሳጣን ለችግሮች ሁሉ፣ በተለይ “በውሃና በመብራት እንዲሁም በቴሌ አገልግሎት ድክመት ላይ ለውጥ እናመጣለን” እያሉ በምርጫ ሰሞን ሲያሰለቹን የነበሩት የፌዴራልና የከተማዋ ባለሥልጣናት የት ገብተው ይሆን? ወይስ ቃልአባይ ሆኑ?

Published in ባህል

                  አሁን አለን በመኪናችን ውስጥ ሆኖ መንገዱን እየመራን የሚገኘው ጓደኛችን አክሊሉ ጉላይ፡፡ አሁን ዛላንበሳ ከተማ ውስጥ ነው የምንገኘው፡፡ ወደ ዋነኛው የጉዞአችን መዳረሻ አሊቴና ለመድረስ ሁለት አማራጭ መንገዶች አሉን፡፡ አንደኛውና የተለመደው መንገድ ለተወሰኑ ደቂቃዎች የኤርትራን ግዛት አቋርጠን ተመልሰን የምንወጣበት መንገድ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ወደ ኤርትራ ሳንገባ ወደፊት በቀጥታ የምንጓዝበት መንገድ ነው፡፡ ይኸኛው የቀጥታ መንገድ በቅርብ ጊዜ ከመሰራቱ በፊት ግን ሁልጊዜ ወደ አሊቲና ሲኬድ ለተወሰኑ ደቂቃዎች በኤርትራ ክልል ውስጥ ማለፉ የግድ ነበረ ሲልም አከለልን፡፡ “ታዲያ በየትኛው መንገድ ብንሄድ ይሻላል?” ሲልም ምርጫ አቀረበልን፡፡ ለጉዞ በተከራየነው መኪና ውስጥ የነበርነው 8 ተጓዦች እርስ በርሳችን ተያየን፡፡ መቼም በኤርትራ ግዛት ውስጥ አልፈን ጉዞ አድርገናል ብንል ነው የተሻለ የሰው ጆሮ ለማግኘት የሚያስችለን፡፡

ሆኖም ግን ደጋግመን በምንሰማው የኢትዮ-ኤርትራ የድንበር ግጭት ሳቢያ፣ ከሆነ ቦታ በተወነጨፈ ከባድ መሳሪያ ለወሬ ነጋሪ እንኳን ሳንተርፍ ብናልቅስ፣ የሚል ስጋት አጠቃንና ጎመን በጤና ብለን፣ ከስጋት ነፃ በሆነው ቀጠና ጉዞ ወደፊት፡፡
ምንም እንኳን ከአዲስ አበባ የተነሳንበት የጉዞአችን ዓላማ (ሐምሌ 7/2005 ዓ.ም) የወዳጃችንን የአክሊሉ ጉላይን የሰርግ ስነ-ስርዓት ለማጀብና በሚዜነት ለማገልገል ቢሆንም መዳረሻችን ግን የአዲ ኢሮብ ማህበረሰብ የሚኖርባት አሊቲና ከተማ ነች፡፡ ይህቺ ከተማ የኢህአፓ የትጥቅ ትግል ሲካሄድበት የነበረው የአሲንባ ተራራና የዘመናችን የኢትዮ-ኤርትራ ከባድ ውጊያ የተደረገበት የአይጋ ተራራ መገኛ ናት፡፡ በዚህች ከተማ ከኢህአፓ መስራቾች አንዱ እንደሆነ የሚነገርለት ዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ ተወልዷል፡፡ በአሊቲና ቆይታችን አንዱ ፕሮግራማችን የሚሆነው የዚህኑ የቀድሞ ታጋይ አባት አቶ ደበሳይን ማግኘትና መተዋወቅ ነው፡፡ ከዚያም ወደ አሲንባና አይጋ ተራሮች ወጥቶ ስለሁለቱም ዘመናት ትዝታዎች የምናውቀውን ያህል ማውጋት! ከነዋሪዎችም ታሪክ መቅዳት! …እጅግ አጓጊ ጉዞ ነው፡፡
የአዲ ኢሮብ ማህበረሰብ ተወላጅ የሆነውንና አሁን ግን በዘላቂነት አዲስ አበባ የሚኖረውን ሙሽራችንን ይዘን እዚያው ተወልዳ ያደገቺውን ሙሽሪትን ከሰርግ በኋላ ወደ አዲስ አበባ ልናመጣ እተጓዝን ነው፡፡

ጉዟችንን በይበልጥ የሰመረ ለማድረግ በአንዳንድ ታሪካዊ ስፍራዎች ለምን ጉብኝት እያደረግን አንሄድም የሚል የተቀደሰ ሃሳብ አመጣንና ባህርዳርን፤ ጎንደርን፤ አክሱምን፤ አድዋን፤ሽሬ እምደስላሴንና አዲግራትን ተራ በተራ እየጎበኘን፣ በቂ ጊዜ ወስደንም ታሪካቸውን እያጠናንና እየተዝናናን፣ አሁን ዛላንበሳ ከተማ ደርሰናል፡፡ እዚህ ጋ ነው እንግዲህ ለአፍታ ወደ ኤርትራ ገባ ብላ በፍጥነት የምትወጣዋ መንገድ ያለችው፡፡
ጉዞአችንን ያሳመረው የሙሽራው የአክሊሉ ጉላይ ወዳጆች የሆንን 8ቱ አጃቢዎቹ በተለያየ ሙያ ላይ የተሰማራን መሆናችን ነበር፡፡ ይህም እርስ-በርሳችን ልምድ እንድንለዋወጥና መንገዳችን አሰልቺ እንዳይሆንብን ማዋዣ ለመፍጠር አግዞናል፡፡ ከዛላአንበሳ ቀጥሎ ወደ አሊቲና ለመድረስ ብዙም ኪሎ ሜትሮች አልቀሩንም፡፡ የበለጠ ግን የሚያስደንቀው አሊቲና ከደረስን በኋላ የ3 ሰዓት ጉዞ ብናደርግ በቀጥታ ወደ ኤርትራ እንደምንገባ መስማታችን ነው፡፡ መቼም የኢትዮ-ኤርትራ ጉዳይ ስሜት የማይሰጠው አገር ወዳድ የለምና እኛም የእነዚህን አገሮች ጦርነት በትዝታ እያስታወስን፤ ስለወደፊት ዕጣ ፈንታቸውም የመሰለንን እየገመትን ሃዘንና ተስፋ እየተፈራረቁብን፣ ወደ ጉዞአችን ማሳረጊያ አሊቴና ገሰገስን፡፡ ብዙዎቻችን ኢትዮጵያና ኤርትራ እንዲህ አንድ መሬት አንድ አፈር ተጋርተው እንደኖሩት ሁሉ ወደፊት ተለያይተው እንደማይቀሩ ተነበይን፡፡

ሌሎቻችን ደግሞ ኢትዮጵያና ኤርትራ ቢታረቁ በፍጥነት ኤርትራ ሄደን መጎብኘት እንደምንፈልግ ምኞታችንን ገለፅን፡፡ የፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ የኤርትራ ጉዳይና የዶ/ር ያዕቆብ አሰብ የማናት የሚሉት መፅሃፍትም በተረዳነው መጠን ለትንታኔ ቀረቡ፡፡ ደስ የሚል ጉዞ ነው፡፡ የባህር ዳር፤ የጎንደርና የአክሱም ጉብኝታችን ለረጅሙ ጉዞአችን አለመሰልቸት ከፍተኛውን አስተዋፅኦ ስላደረጉልን በጉዞአችን ላይ መሰልቸት የሚባል ነገር ቦታ አልነበረውም፡፡ የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ይበልጡኑ ያስተዋወቀኝን ዛላንበሳን በመኪና ላቋርጣት ስላልፈለግሁኝ ከመኪናችን ወርጄ በግምት ለ10 ደቂቃ በአስፋልቱ ላይ በሶምሶማ በመሮጥ፣ ባንድ ወቅት እልም ያለ ጦርነት የነበረባት ይህች ዛላንበሳ ከተማ ዛሬ የሰላም አየር እየተነፈሰች የመሆኑዋን ደስታ ተጋራሁ፡፡ መኪናችንም ቀስ እያለ በመከተል አጀበኝ፡፡ እንዲህ እየተዝናናን ወደ ጉዞአችን መዳረሻ አሊቲና ከተማ በሰላምና በጤና ገባን፡፡
እዚህ ጋር የእኔን ጽሁፍ ቆም ለማድረግ እገደድና በቅርቡ ካነበብኩት የአሲንባ ፍቅር ከሚል በደራሲ ካሕሳይ አብር ብስራት ከተፃፈ መፅሃፍ ላይ የአዲ ኢሮብን ማህበረሰብና የአሊቴና ከተማን ጥሩ አድርጎ የሚያስተዋውቀውን ጥቂት አንቀፅ በአስረጂነት በመጥቀስ፣ እናንተ ውድ አንባቢዎቼ በታሪክ አጋጣሚ ስለተገኘሁባት ከተማ ያላችሁን ግንዛቤ በመጠኑ ከፍ ለማድረግ አሰብኩ፡፡
የአዲ ኢሮብ ህዝብ የመቻቻል፤ የእንግዳ ተቀባይነት፤ የህዝብና የታጋይ አንድነት ፍቱን ዓርአያ ነው፡፡ አዲ ኢሮብ በትግራይ ክልል ሰሜን ምስራቅ በአጋሜ አውራጃ ከአዲግራት ከተማ በስተምስራቅ የሚገኝ አብዛኛውን ተራራማ የሆነ ወረዳ ነው፡፡ የአካባቢው ሰዎች እንደሚሉት፣ ኢሮብ የሚለው ቃል የመጣው ኢሮባ ከሚለው ሲሆን ይህም በሳሆ ቋንቋ ወደ ቤት ግቡ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የማህበረሰቡ ስያሜ ምንጭ ኢሮብ ህዝብ እንግዳ ተቀባይ፤ ኑ ግቡ፤ ብሉ፤ ጠጡ የሚል ደግና የዋህ ህብረተሰብ ከመሆኑ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ከአዲ ኢሮብ ተራራዎች ትልቁ ከፍተኛ ቦታ የአሲንባ ተራራ ጫፍ ነው፡፡

አሲንባ ማለት ቀይ አምባ ማለት ሲሆን የዚህ ተራራ ከፍታ 3250 ሜትር ነው፡፡
የኢሮብ ህዝብ ውጊያ የማይፈራ፤ ያገኘውን ተካፍሎ የሚበላ፤ ያመነውን በፍፁም አሳልፎ የማይሰጥ፤ እስከተፈለገው ጊዜ ደብቆና ጠብቆ የሚያቆይ፤ ህዝብ ነው፡፤ የኢሮብ ህዝብ ካመነ አመነ ነው፡፡ የኢሮብ ወረዳ ባህላዊ ከተማ በሆነችው አሊቲና ውስጥ የሚገኘው በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን የተመሰረተው በ1840 ዓ.ም ሲሆን በቤተክርስቲያኑ ስር የተመሰረተ ዘመናዊ ት/ቤትም አለ፡፡ ይህ ት/ቤት ከተመሰረተ ጀምሮ ነፃ የትምህርት ዕድል እየሰጣቸው ወደ ሮም የሄዱ በርካታ የአካባቢው ተማሪዎች አሉ፡፡ ከእነዚህም ተማሪዎች መካከል ወደ ተለያዩ የአውሮፓ አገሮች ሄደው በልዩ-ልዩ የሞያ መስኮች ትምህርታቸውን ለመከታተል የቻሉ አሉ፡፡ ከቀደምት የኢትዮጵያ ተማሪዎች መካከል በዚህ የካቶሊክ ሚሽን ት/ቤት ተምረው ከፍተኛ የትምህርት ዕድል ካገኙት አንዱ የኢህአፓ መስራችና የማዕከላዊ ኮሚቴና የፖሊት ቢሮ አባል የነበረው ዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ ይጠቀሳል፡፡ (የአሲንባ ፍቅር ገፅ 53-56 ከተጠቀሱት ውስጥ የተቀነጨበ)
አሊቲና የደረስነው ከሰርጉ ቀን አንድ ሳምንት ቀደም ብለን ስለነበረ ከከተማው ሰው ጋር የመገናኘቱ፤ ወደ አይጋ ተራራ የመውጣቱንና ወደ አሲንባ ተራራ ቀርበን ፎቶ የመነሳቱን ዕድል አግኝተናል፡፡
በዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ አባት መኖሪ ቤት
የአሲንባ ፍቅር መፅሃፍ ደራሲ ካህሳይ የዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይን ታሪክ ስሙን ብቻ ከመጥቀስ ውጪ በመፅሃፉ ላይ ቦታ ሰጥቶ አልገለፀውም፡፡ ዶ/ሩ እንዳለመታደል ሆኖም በአሊቴና ነዋሪዎች ዘንድ ታሪኩ በሚፈለገው መልኩ አይታወቅም፡፡ በተለይ የከተማዋ ነዋሪ የሆኑ ወጣቶች ስለ ተስፋዬ የሚያውቁት ነገር ከታጋይነቱ ውጪ እምብዛም ሆኖ በማግኘታችን በወጣቶቹ መሪነት ወደ አቶ ደበሳይ ወላጅ አባቱ ቤት አመራን፡፡ እቤት ስንደርስ አንድ ወጣት ልጅ በሳሎን ውስጥ ተቀምጦ የአረብ ዲሽ ሲመለከት አገኘነው፡፡ ከአዲስ አበባ የመጣን ዕንግዶች መሆናችንንና አቦይ ደበሳይን ለማግኘትና ለመተዋወቅ፤ ስለልጃቸው ተስፋዬም የሚነግሩንን ለመስማት የተገኘን መሆኑን ነገርነው፡፡ ወጣቱም አቦይ ደበሳይ ትንሽ አመም አደርጎአቸው በቤቱ ሌላኛው ክፍል መተኛታቸውን ነግሮን፣ እስኪ ከተነሳ ልይላችሁ በማለት ወደ ሌላኛው ክፍል አመራ፡፡
ከትንሽ ቆይታ በኋላም ተመለሰና አባባ ተኝቷል፤ አልተነሳም አለን፡፡

እርሳቸውን በአካል የማየትና ቢቻልም የመተዋወቃችን ጉጉቱ ስላየለብን አንድ ጊዜ በተኙበት ልናያቸው ብንችል፤ ደግሞም ለእርሳቸው ያመጣንላቸው ስጦታ ስላለ እርሱንም ብናበረክትላቸው በማለት አበክረን ስለጠየቅነው ወጣቱ በፍፁም የአክብሮት ስሜት ተከተሉኝ ብሎን ወደ አባባ ደበሳይ መኝታ ክፍል ይዞን ሄደ፡፡
ሁላችንም እዚህ ከመምጣታችን በፊት ማርጀታቸውን ብንሰማም በዚህ ሁናቴ እናገኛቸዋለን ብለን ባለማሰባችን አልጋ ላይ ድንገት ባየነው ነገር በእጅጉ ተደናገጥን፡፡ አቶ ደበሳይ እንካንስ እኛን ተቀብለው ለመተዋወቅና የልጃቸውን ታሪክ ለመንገር ይቅርና ከአንገታቸው እንኳን ቀና ለማለት የማይችሉ፤ ሰውነታቸው እጅግ ከመክሳቱ የተነሳ አልጋው ላይ ብርድ ልብስ እንጂ ሰው ያለበት የማይመስል፤ በሽታው፤ ሃዘንና ዕድሜ ባንድ ላይ አብሮ ያደቀቃቸው ሰው ሆነው አገኘናቸው፡፡ ከዚህ በኋላ እኒህን ምስኪን ሰው አንዳችም ነገር ለማስቸገር ፍላጎቱ ስላልነበረን ወሬአችን እንዳይረብሻቸው በማሰብ ክፍላቸውን ጥለን ወጣን፡፡

በዚህ ጊዜ ወጣቱ ልጅ ከጎኑ ሆነው አባታቸውን ወደሚያስታምሙት አንዲት ሴት ወይዘሮ ዞር ብሎ የተስፋዬ ታናሽ እህት ናት በማለት አስተዋወቀን፡፡ እኛም በመተዋወቃችን የተሰማንን ደስታ ከገለፅን በኋላ፣ ዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይ ከዚያች ትንሽ ከተማ አሊቴና ወጥቶ ኢህአፓ የሚባለውን በታሪክ በእጅጉ የሚታወቀውን ኢህአፓን ከትግል አጋሮቹ ጋር መስርቶ በሞት እስከተለየበት ጊዜ ድረስ የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች ከነበሩት ውስጥ አንዱ የነበረ መሆኑን በማስታወስ፣ የልጅነት ባህሪው እንዴት እንደነበረና ከአሲንባ በኋላ ከቤተሰቡ ጋር ስለነበረው ግንኙነት ወይዘሮዋን ጠየቅናቸው፡፡
ሴቲቱ የሚናገሩትን የኢሮብ ማህበረሰብ ቋንቋ ለመስማት ባንታደልም ትረካንው በራሳቸው ልሳን ብናደምጠው መልካም እንደነበረ በመጓጓት በወጣቱ አስተርጓሚ አማካኝነት አንዳንድ መረጃዎችን አገኘን፡፡

እንደ ወይዘሮዋ አባባል ተስፋዬ ደበሳይ ገና በልጅነቱ በካቶሊክ ሚሽን ትምህርት ቤት የተማረና እዚያው ያደገ በመሆኑ ከቤተሰቡ ጋር ብዙ እንዳልኖረ፣ ከፍ ሲልም ውጪ ሄዶ ተምሮ እንደመጣና ከዚያ በአሲንባና በሌሎችም ስፍራዎች በትግል ውስጥ ያሳለፈ በመሆኑ ከእርሳቸው ጋር ብዙም አይተዋወቁም፡፡ ሆኖም ግን አባታቸው አቦይ ደበሳይ ተስፋዬ አሲንባ በነበረበት ጊዜ በተደጋጋሚ በድብቅ እየሄዱ እንደጎበኙትና አንዳንድ ጨዋታዎችን እንደተጫወቱ አስረዱን፡፡ የአቦይ ታሞ ከአልጋ ላይ መውደቅ ይበልጡኑ የሚያስቆጨው የዚህን ጊዜ ነው፡፡ ታሪክ የመዘገብና ቢያንስ እንኳን ጫር ጫር አድርጎ የማስቀመጡ ልማድ የሌለን ህዝቦች ነንና የእነዚህ አባትና ልጅ የበረሃ የአንዳንድ ነገሮች ጨዋታ ምን እንደነበር ሳይከተብ እንደዚሁ ተድበስብሶ መቅረቱ በእጅጉ ያስቆጫል፡፡ የሆነው ሆኖ የተስፋዬን በትልቁ የታጠቡ ፎቶዎች ይዘን ከእህቱ ጋር የመታሰቢያ ፎቶ ከተነሳን በኋላ ተሰነባብተን ተለያየን፡፡ በዚህ አጋጣሚ አቦይ ደበሳይ ተገቢውን የህክምና ድጋፍ እንዲያገኙ ዘመድ ወዳጆቻቸው አንዳች ነገር ማድረግ ቢችሉ መልካም ነው እላለሁ፡፡
አሲንባ/አይጋ
አሲንባና አይጋ እነዚህ ሁለት ተራሮች የጦርነትም ቢሆን በታሪክ ያላቸው ትውስታ ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ የአሲንባ ፍቅር በሚለው መፅሃፍ ላይ ታሪኩ በስፋት እንደተገለፀው፣ የአሲንባ ትግል ተሳክቶ ቢሆን ኖሮ ደደቢት እንደሚባለው የእግር ካስ ቡድን አሲንባ የሚባልም ይኖረን እንደነበር እሙን ነው፡፡ አሲንባ የኢህአፓ ጓዶች በርካታ የአይዲዮሎጂ ፉክቻ ያደረጉበትና የትጥቅ ትግላቸውንም ያደራጁበት እንደመሆኑ ለአሊቲና ነዋሪዎች ያለው ትዝታ በደብዛዛውም ቢሆን ለረጅም ዓመታት አብሮአቸው የሚኖር ነው፡፡ ለእነርሱ ግን የቅርብ ጊዜ ዘግናኝ ትዝታቸው በአይጋ ተራራ ላይ የተደረገው የኢትዮ ኤርትራ ከባድ ጦርነት ነው፡፡ ለሙሽራው ክብር ከሰርጉ ቀደም ብሎ አቶ ግደይ በተባሉ የቅርብ ዘመዱ በተዘጋጀ የምሳ ግብዣ ላይ ለመገኘት ሙሽራውን አጅበን የአቦይ ግደይ መኖሪያ አቅራቢያ አካባቢ ወደሚገኘው አይጋ ተራራ ወጥተናል፡፡
ስፍራው ስንደርስ በአቦይ ግደይ ቤት ቁጥራቸው ከ30 በላይ የሆኑ የመከላከያ ሰራዊት አባላት ዩኒፎርማቸውን እንደለበሱ የግብዣው ተካፋይ ሆነው ሲበሉና ሲጠጡ አገኘናቸው፡፡ በሁኔታው ግራ ተጋብተን ምንድነው ነገሩ ብለን ስንጠይቅ፣ ድንበር ጠባቂዎች መሆናቸውንና ሁልጊዜ የአካባቢው ሰው እንዲህ ዓይነት ፕሮግራም ሲያዘጋጅ የመከላከያ ሰራዊት አባላቱን ታሳቢ አድርጎ ሰፋ ያለ ድግስ እንደሚያዘጋጅ ተነገረን፡፡ በዚህ ጊዜ አንድ ሃሳብ ወደ አእምሮዬ ከተፍ አለ፡፡ ስለድንበር ጠባቂዎች!
ድንበር አስከባሪዎች፤ ኬላ ጠባቂዎች ወዘተ---እነዚህ ሰዎች በከፍተኛ ሁኔታ ለአደጋ የተጋለጡ ናቸው፡፡ በአካባቢው አንድ ዓይነት ፀብ ሲነሳ የመጀመሪያዎቹ ገፈት ቀማሽ የሚሆኑት እነሱ ናቸው፡፡ ብዙ ጊዜ እነርሱ ወደሰፈሩበት አካባቢ የሚመጣ ሰው የለምና ሰው ይናፍቃቸዋል መሰለኝ በተለይ ከመሃል አገር የመጣ ሰው ሲያገኙ በከፍተኛ አክብሮት ሊያጫውቱት ይፈልጋሉ፡፡ የዕለት ተልዕኮአችንን አሳክተን እኛ በየቤታችን ተረጋግተን ስንተኛ፣ በህይወት አጋጣሚ ድንበር ጠባቂ የሆኑ ወታደሮች ግን ቀን ተሌት ተግተው ድንበራችንን የማስከበር ኃላፊነታቸውን እየተወጡ ይገኛሉ፡፡

አብዛኞቹ ሲጋራ ያጨሳሉ፡፡ ወጣቶች ቢሆኑም ሰውነታቸው ግን የፈረጠመ ነው፡፡ ከእነዚህ ሰዎች እንደ አንዱ ብሆንስ ብዬ ራሴን ላፍታ በጀግንነት ልመዝነው አሰብኩና ፈፅሞ ሊሆንልኝ የማይችል ቅዠት ነገር ሲሆንብኝ ጊዜ ተውኩት፡፡
ደጉ የኢሮብ ማህበረሰብ መቼም ተበልቶና ተጠጥቶ የሚጠገብ አይመስለውምና ከዚህ በፊት አይቼው በማላውቀው አይነት እየተጠበሰ የሚቀርብ አስገራሚ የስጋ ጥብስ እየጋበዘን፣ ማወራረጃውንም ጠጅ እንደ ጉድ እያቀረበልን ስንጫወት ቆይተን፣ የሁላችንም ጉጉት ነበረና በአይጋ ተራራ ላይ ስለተደረገው የኢትዮ-ኤርትራ ከባድ ጦርነት ወሬ ተጀመረ፡፡ ሁሉም የድንበር ጠባቂዎች ስለዚህ ቦታ ልዩ ትዝታ አላቸው፡፡ በወቅቱ በስፍራው ያልነበሩትም ቢሆኑ በአካባቢው የነበረውን ከባድ ጦርነት በታሪክ ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡ አመጣጣችን ለሰርግ ቢሆንም እነሆይ ጦርነቱም የታሪካችን አንዱ አካልና መጥፎም ጠባሳችንም ነውና በርካታ ሰዎች ስላለቁበት የእጅ በእጅ ውጊያ ፊልም በሚመስል ሁኔታ የተተረከልንን አደመጥን፡፡ ከዚህ ካለንበት የአይጋ ተራራ ሆነን ፊት ለፊት ስንመለከት ደግሞ የአሲንባ ተራራ ቁልል ብሎ ገዝፎ እርሱም የራሱን የታሪክ ትዝታ እያስነበበን እንመለከተዋለን፡፡ ይህንን ጊዜ ስለዚህ መከራ ቻይና ደግ ማህበረሰብ በጥልቀት ሳያስቡ መቅረት ፈፅሞ የማይቻል ነገር ነው፡፡
189 አባወራዎችን ድንገት የተነጠቁት አዲ ኢሮቦች
ከማህበረሰቡ አባላትና ያገር ሽማግሌዎች ጋር ሰፊ ውይይት ሳደርግና በተለይም በጋዜጠኝነት ዓለም ውስጥ ያለሁ መሆኔን ሲረዱ፣አፅንኦት ሰጥተው የነገሩኝ ነገር በእጅጉ ስሜቴን ነክቶታል፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት ይህቺ የአሊቲና ከተማ በኤርትራ ቁጥጥር ስር ውላ ስለነበረ ከከተማዋና ከአጎራባች አካባቢዎች 189 አባወራዎች ከቤታቸው እየተጠሩ በኤርትራ ወታደሮች ተወስደዋል፡፡ ጦርነቱ በኢትዮጵያ አሸናፊነት ቢደመደምም እነኚህ ከቤታቸው ተጠርተው የተወሰዱ ሰዎች እስካሁን ድረስ የት እንደገቡ ሳይታወቅ ቀርቷ፡፡ እንደ አገር ሽማግሌዎቹ አባባል፣ ወገኖቻቸው ሞተውም ከሆነ ቁርጣቸውን አውቀው እርም ለማውጣት እንኳን አልተቻለም፡፡ የእነዚሁ የት እንደገቡ ያልታወቁ ሰዎች ስም ዝርዝርን ይዘው ወደተለያዩ የመንግስት አካላት ዘንድ ሄደው አቤት ቢሉም እንዲህ ነው ነገሩ የሚላቸው አላገኙም፡፡ በዚህም የማህበረሰቡ አባላት እስካሁንም ድረስ በከፍተኛ ሃዘን ላይ መሆናቸውን በምሬት ነግረውኛል፡፡ አሁንም ቢሆን መንግስትና የሚመለከታቸው አካላት አንድ ነገር በዚህ ጉዳይ ላይ እንደሚያደርጉላቸው በተስፋ ይጠባበቃሉ፡፡ በነገራችን ላይ አሊቲና ዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይን ጨምሮ በልዩ-ልዩ ትምህርቶች ስፔሻላይዝድ ያደረጉ ከ10 የማያንሱ ዶክተሮችንም አፍርታለች፡፡ እነማን እንደሆኑም ያገር ሽማግሌዎች በስሜት ተውጠው አጫውተውኛል፡፡
እንደተፃፈላት ያገኘሁዋት ከተማ አሊቴና
የአሲንባ ፍቅር መፅሃፍ ሰፋ ያለ ገፅ ሰጥቶ (ከገፅ 55 እስከ 57 ድረስ) በዝርዝር ፅፎ ያስተዋወቀኝን ታሪክ በዓይኔ ለማየት ታድያለሁ፡፡ እነዚህ የማህበረሰብ አካላት በእርግጥም እጅግ ደግና ጨዋዎች ናቸው፡፡ በከተማዋ ያለው ነዋሪ አብዛኛውን የካቶሊክ ዕምነት ተከታይ ሲሆን በስፍራው ቡና ቤትም ሆነ በሴተኛ አዳሪነት የሚተዳደሩ ሴቶች የሉም፡፡ ከተማዋ ውስጥ ፈፅሞ ጫት አይቃምም፡፡ ጫት መሸጫም የለም፡፡ ጠላ ቤቶችና ጠጅ ቤቶች ግን በቁጥር ትንሽ ቢሆኑም አግኝተናል፡፡
በእርግጥ ከአሲንባ ጊዜ ጀምሮ እስከ ኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ድረስ ወታደር አዘወትሮ የሚጎበኛት ከተማ ናትና አሊቲና በሲጋራ አጫሾች ቁጥር አትታማም፡፡ በርካታ ወጣትና አዛውንት ሲጋራ አጫሾች በብዛት በከተማዋ አሉ፡፡ ወጣቶቹ በእጅጉ ሰው ወዳዶች ሲሆኑ ቀን-በቀን የበለስ ግብዣ በማድረግ ሲንከባከቡን ሰንብተዋል፡፡ ለምለም የተባለች አንዲት እንደ ካፌ ነገር ያላት ሴት ከባለቤትዋ ዕቁባይ ጋር ስጋ ሲሰለቸን እጅግ የሚጣፍጥ መኮረኒና ፓስታ ትሰራልን ነበረ፡፡ የአዲ ኢሮብ ማህበረሰብ የጥህሎና የስጋ ስፔሻሊስት ነው፡፡ ጥህሎ ሲሰሩና ስጋ ሲጠብሱ እጅ የሚያስቆረጥም አድርገው ነው፡፡ የሰርግም ሆነ የሃዘን ስነ-ስርዓታቸው በጋራ የሚከወን ነው፡፡ ማርና ቅቤያቸውም የተለየ ነው፡፡ ኢሮብ ውስጥ ማርና ቅቤ ግን አይሸጥም፡፡ ማህበረሰቡ ራሱ ነው በስጦታ የሚያቀርብልህ እንጂ!
ቢግ ብራዘር አሊቲና
በአሊቲና ሆቴል የሚባል ነገር የለምና ያረፍነው የማህበረሰቡ ተወላጅ ከሆነውና የሙሽራው የቅርብ ዘመድ ከሆነው ከዳንኤል እናት ቤት ሲሆን ወ/ሮ አብረኸት ቤታቸውን ለቅቀው ከ10 ቀን በላይ እጅግ ሊነገር ከሚችለው በላይ በሆነ መስተንግዶ ሲንከባከቡን ከርመዋል፡፡ 8 ከተለያየ ሞያዎች የመጣን በተለያየ የዕድሜና የኑሮ ደረጃ ላይም የምንገኝ የሙሽራው ወዳጆች እኛ ቢግ ብራዘር አሊቲና ብለን የጠራነው የነዳንኤል/የእነ ወ/ሮ አብርሃት ቤት በርካታ ትዝታዎችን በውስጣችን ቀርፆብናል፡፡ መብራት ካልጠፋ ዕንቅልፍ አይወስደንም የሚሉ፤ ፕሮፌሽናል ሰዎች 4 ሰዓት ብቻ ነው የሚተኙት በሚል የግል ፍልስፍና እንቅልፍ የማይተኙና ሲያነቡ የሚያድሩ፤ በሌሊት ለዎክ ካልወጣን ብለው የሚያስቸግሩ፤ የአይፓድ ፊልም ሱስ የተጠናወታቸው፤ ጠጥተው ሞቅ ሲላቸው ሌላውን አላስተኛ የሚሉ፤ የልጅነት ትዝታቸውን ሲያወሩ በዕንባ የሚታጠቡ፤ ወዘተ እነዚህ ሁሉ የቢግ ብራዘር አሊቲና ዋና ዋና ትዝታዎቻችን ናቸው፡፡ ለእኛም የዩኒቨርሲቲን ዶርሜተሪ የሚያስታውስ ከ10 ያላነሱ ተከታታይ ቀናትን በመቻቻል ያሳለፍንበት የአዲ ኢሮብ ትዝታችን ብዙ ነው፡፡ በተደጋጋሚ ወደ ወንዝ እየወረድን ገላችንን ተለቃልቀናል፡፡ በግ አርደን በጫካ ውስጥ ካምፕፋየር አድርገናል፡፡ ተራራ በእግራችን መውጣት ተለማምደናል፡፡ የኢሮብና የትግሬኛ ቋንቋ ለመስማት ከሳምንት በላይ ልምምድ አድርገናል፡፡

ከማህበረሰቡ አባላት ጋር በጠላና ጠጅ ቤቶች ለረጅም ሰዓት አብረን ተቀምጠን ወግ ጠርቀናል፡፡ ከነዋሪ ወጣቶች ጋር ጠዋትና አመሻሹ ላይ የእግር ካስ ግጥሚያ አድርገን በሰፊ ውጤት ተሸንፈናል፡፡ በእነ ፀጋ ቤት የቡና ጠጡ ፕሮግራም አካሂደናል፡፡ የኢህአፓ አባል እንደነበሩ ካጫወቱን ከመምህር ተስፋዬ ጋር (እሳቸው ያገቡት የዶ/ር ተስፋዬ ደበሳይን ሌላ እህት ነው) ተራራ ላይ ቁጭ ብለን ጣፋጭ የህይወት ታሪካቸውን አድምጠናል፡፡ የኢሮብ ዋና ከተማ በሆነችው ዳውሃን ተገኝተን በቀዝቃዛ ቢራ አንጀታችንን አርሰናል፡፡ ብቻ አሊቲናን ድምቅ አድርገናት ተመልሰናል፡፡ ጉዟችን ደግሞ እጅግ አዝናኝ እንዲሆን የሳቅ ምንጫችን የነበረው የቀድሞ የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ወጋ-ወጋ በፈገግታ ዓምድ ፀሃፊ ጀቤሳ/ ቢኒያም እሸቱ የነበረው አስተዋፅኦ ሊጠቀስ የሚገባው ነው፡፡
በነገራችን ላይ እዚያ በቆየንበት ወቅትም እንደ አጋጣሚ ሆኖ በአንድ የቀብር ስነ-ስርዓትም ላይ ለመገኘት በቅተን ነበረ፡፡ ይህንን አስደናቂ ቀብርና የወዳጃችንን የሰርግ ስነ-ስርዓት በተመለከተ እንደዚሁም በጉዞአችን ላይ በአዲግራት ከተማ ስለተመለከትኩት የኦርቶዶክስ፤ የሙስሊምና የካቶሊክ ሃይማኖቶች ጥምረት የሆነ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት፣ በሰላም ዙሪያ ስለሚሰራው አስደናቂ ስራዎች በወደፊት ፅሁፌ በስፋት የምመለስበት ይሆናል፡፡ በመጨረሻም ግብዣ!
የአዲ ኢሮብ ማህበረሰብ በአሊቲና ከተማ የመስቀል በዓልን በየዓመቱ እጅግ ደማቅ በሆነ ስነ-ስርዓት እንደሚያከብር የአገር ሽማግሌዎችና የአካባቢው ተወላጆች ነግረውኛል፡፡ በመሆኑም እንግዶች ከየአካባቢው በመገኘት ማህበረሰቡን እንዲያውቁትና ታሪኩንና ባህሉንም እንዲገነዘቡለት ማህበረሰቡ በደግነት ግብዣውን እንዳቀርብ አዞኛል፡፡ እኔም ትዕዛዙን አክብሬ እነሆ አስታውቄአለሁ፡፡ ለመጪው መስቀል ወደዚያው በድጋሚ ማምራቴ አይቀርምና የጉዞው ሃሳብ ያላችሁ ሰዎች ለምን አንገናኝም? መልካም ቅዳሜ!

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 24 August 2013 10:32

“የማያውቁት አገር…”

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ዝናቡን አሳንሶ ውርጩን ላከብን አይደል! አየሩ ውርጭ፣ ኑሮው ውርጭ…
እትቱ በረደኝ ብርድ ይበርዳል ወይ
የማያውቁት አገር ይናፍቃል ወይ?
የሚሏት ዘፈን አለች፡፡ አዎ እንደ ዘንድሮ ሁኔታችን ከሆነ…አለ አይደል… የማያውቁት አገር እንክት አድርጎ ይናፍቃል! ነገሮች ሁሉ ግራ ሲገቡ፣ “የእኔ ጓዳ ከሞላ የሌላው ዳዋ ይምታው…” አይነት አስተሳሰብ ሲበዛ፣ በ‘ማስተዳደር’ እና በ‘መግዛት’ መካከል ያለው ቀጭን መስመር ሲጠፋ፣ አቤቱታ አቅራቢ እንጂ አቤቱታ ተቀባይ ሲጠፋ፣ “የወሎ ህዝብ መሰደድ ልማዱ ነው…” እንዳሉት የድሮ ባለስልጣን… “የኢትዮጵያ ህዝብ ብሶት ማቅረብ ልማዱ ነው…” አይነት ‘ወንበሬም እኔም አንገለበጥም’ አይነት ‘ቦስነት’ ሲበዛ…“እኔን ተከተል…” እንጂ “ጎን ለጎን እንጓዝ…” ማለቱ ለአንደበት ሲጎመዝዝ…ያኔ እንክት አድርጎ የማያውቁት አገር የማይናፍቅሳ!
ስሙኝማ…ሰሞኑን ቢቢሲም አልጀዚራም ስለ ወገኖቻችን ስደት ‘ጉዳችንን’ አደባባይ ሲያወጡብን አያችሁልኝ አይደል! እናማ…አንድ ሆድ ለመሙላት ያን ሁሉ መከራ መጋፈጥ የ‘ጥጋብ’ ሳይሆን ነገርዬው ሁሉ “አገሩ ለባለ አገሩ” አልሆን ብሎ…የማያውቁት አገር እየናፈቀ ነው፡፡
ከዚህ በፊት የጠቀስናትን እንድገማትና… ልጅቱ ዓረብ አገር ለመሄድ ደፋ፣ ቀና ትላለች.. እና ሀሳቧን እንድትለውጥ ሊመክሯት ያስቡና…“እነኚ ሁሉ ሲሞቱ እየሰማሽ ቢቀርብሽ ምን አለ!” ምናምን አይነት ነገር ይሏታል፡፡ ምን ብላ ብትመልስ ጥሩ ነው…“እዚህም ያው ሞት ነው፡፡”
እኔ የምለው… እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ይሄ ሰሞኑን ብዙ የግል ትምህርት ቤቶች እያደረጉ ያሉት ጭማሪ…“እዚህ አገር ‘ሰበብ’ እየተጠበቀ ‘ቆዳ ገፈፋ’ ላይለቀን ነው!” ያሰኛል። ወላጆች አምስት ሳንቲም ተጨማሪ ‘ፈረንካ’ ባላገኙበት፣ ‘ጤፉም ጧፉም’ በየጊዜው ሽቅብ እየተሰቀለ ባለበት ወቅት በአንድ ልጅ የወር ሂሳብ ላይ እስከ ሺህ ብር መጨመር…አለ አይደል… “ኸረ ውሎ አድሮ ጡር ይኖረዋል!” ያሰኛል፡፡ እንደውም “ከፈለጋችሁ ሌላ ረከስ ያለ ትምህርት ቤት ውሰዱ…” አይነት ቃና የሚሰማባቸው አሉ ይባላል፡፡ እናማ…ልጆችን በመልካም መንገድ አንፆ ለማሳደግ ሲያቅት…የማያውቁት አገር የማይናፍቅሳ!
የልጆች ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ስሙኝማ…ትንሹ ልጅ አስቸጋሪ ነው፡፡ እናላችሁ… ብቻውን አውቶብስ ይሳፈርና ከሾፌሩ ጀርባ ይቀመጥና መጮህ ይጀመራል፡፡ “አባዬ በሬ ሆኖ እናቴ ላም ብትሆን ኖሮ እኔ ሚጢጢ በሬ እሆን ነበር!” ሾፌሩ በጣም ይናደዳል፡፡ ልጁም መጮሁን ይቀጥልና… “አባዬ ዝሆን ቢሆንና እናቴ ሴት ዝሆን ብትሆን ኖሮ እኔ ሚጢጢ ዝሆን እሆን ነበር!” ልጁ እንዲህ፣ እንዲህ እያለ መጮሁን ይቀጥላል፡፡
ሾፌሩ በጣም ይናደድና አፉን ለማዘጋት እንዲህ ይለዋል…“አባትህም እናትህም ወፈፌ ቢሆኑ ኖሮስ!” ይለዋል፡፡ ልጁ ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው…“የአወቶብስ ሾፌር እሆን ነበር፡፡” ቂ…ቂ…ቂ…
ደግሞላችሁ…ካነሳነው አይቀር፣ በከተማችን እየተከፈቱ ያሉ አንዳንድ ሬስቱራንቶች…አለ አይደል…ግራ ያጋቧችኋል፡፡ እንዴ… አንዳንዴ እኮ ለአንዲት ‘ስኒ’ ሻይ በፋይቭ ስታር ሆቴል ከሚጠየቀው ሂሳብ እጥፍ የሚደርስ ይጠይቋችኋል፡፡ ሻይ (ያው ሙቅ ውሀና ሻይ ቅጠል!) ሦስትና አራት ባውንድ ሲሆን፣ እንዲህ የሚያደርገው…አለ አይደል… የ‘ማርኬቲንግ ጥበብ’ ሳይሆን የአልጠግብ ባይነት አባዜ…ነው። ሚጢጢዎቹ ቦታዎች ብትሄዱም በሸራፋ ብርጭቆ፣ ስኳሩ ‘ቀበቶን በማጥበቅ’ አይነት ቁጠባ የተጨመረበት ሙቅ ውሀ…ሰባትና ስምንት ብር ይባላል፡፡ እናማ በሰበብ አስባቡ ሁሉም ዋጋ ጭማሪ ሲሆንና፣ ምናምን ማድረግ የማትችሉ ‘ምስኪንነት’ ስሜት ሲያድር …የማያውቁት አገር የማይናፍቅሳ!
የምር ግን… እዚህ አገር የ‘ሴልፊሽነት’ መጠኑና ስፋቱ ለመግለጽም የሚያስቸግር ደረጃ እየደረሰ ነው! ብቻ ምን አለፋችሁ ሁሉም… ከቦሶች እስከ ታች ድረስ ደግሞ “በየት በኩል የቀረችውን ሳንቲም እናራግፋቸው?” እያሉ እንቅልፍ አጥተው የሚያድሩ አይመስላችሁም!
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ለምሳሌ በእኛ አገር ‘ቦተሊካ’ ላይ ‘ሰበብ’ ሲገኝ…አለ አይደል… “የጫማህ ማስቀመጫ ያድርገኝ!” አይነት ይል የነበረው ሁሉ… “ከእነ እንትና ጋር አረቄ እንደምትጠጣ የማናውቅ መሰለህ!” አይነት ‘ቆዳ ገፈፋ’ ይጀመርላችኋል፡፡
ደግሞላችሁ…ምሁራን አካባቢ ካያችሁ “እሱ እኮ የአይንስታይን ደቀ መዝሙር መሆን የሚችል ነው…” ለማለት ጥቂት ይቀራቸው ያልነበረውን ሰው…አለ አይደል…‘ሰበብ’ ሲገኝ ምን አይነት ‘ቆዳ ገፈፋ’ ይጀመር መሰላችሁ… “እኔ’ኮ ልደርስበት ያልቻልኩት ዶክትሬቱን ፎርጅድ ያሠራው የት እንደሆነ ነው እንጂ ወረቀቷማ ፌክ ነች!” ይባላል፡፡
አሪፍ የነበረችው እንትናዬ አለችላችሁ…“ልቅም ያለች ልዕልት ዲያናን የምታስንቅ ቆንጆ…” ስተባል የነበረችው ፈዘዝ ስትልና ‘ሰበብ’ ሲገኝ ያው አድናቂ ሰራዊት ምን ማለት ይጀምራል መሰላችሁ…“ድሮም እኮ ዕድሜ ለሜክ አፕ ትበል!” አይነት ነገር ይመጣል፡፡
እናማ እንደዚህ አይነት ነገሮች ሲበዙ፣ ከሰው መርጦ ለሹመት፣ ከእንጨት መርጦ ለታቦት ማለት ሲያቅተን…ምነው የማያውቁት አገር የማይናፍቅሳ!
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…እዚቹ ከተማችን ውስጥ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ እየተፈጠሩ ያሉ ነገሮች…አለ አይደል…አያሳስቧችሁም? እንዴት ነው በአጭር ጊዜ ውስጥ ሁሉም ነገር እስከ ጽንፍ እየሄደ የሚበላሸው ያሰኛል፡፡ እናላችሁ…መጪ ትውልዶች ላይ እንደ ዴሞስቴን ሰይፍ የተንጠለጠሉ ችግሮች እንዲህ ሲከማቹ…የሚጨንቃቸው ቦሶች የማንሰማሳ! …“ለምንድነው ደግ፣ ደግ ነገሮችን መያዝ ያቃተን!” የሚል የአገር አለኝታ ምነው ጠፋሳ! ሁሉም ነገር የ‘ቦተሊካ ቲራቲር’ እየሆነ ምድር ለምድር እየተስፋፉ ትውልድ እየበከሉ ያሉ ነገሮች ችላ ሲባሉ…አለ አይደል...የማያውቁት አገር የማይናፍቅሳ!
አንዳንድ ጊዜ ወላጆች…አለ አይደል… “እንደው ልጆቼ እንደምንም ብለው ከዚህ አገር ቢወጡልኝ…” ሲሉ…ልጆቻቸው ‘የውጪ ዜጋ’ እንዲሆኑላቸው የመመኘት ጉዳይ ሳይሆን “ዓይኔ እያየ ገደል ሲገባ ዝም ብዬ አላይም…” በሚል በየቦታው ከሚገማሸሩ የጥፋት ማዕበሎች ሊከላከሏቸው ነው፡፡
ታዲያላችሁ…‘የማያውቁት አገር የሚያስናፍቁ’ ነገሮች ሲበዙ…ይመለከተኛል ባይ ሲጠፋ የምር ጥሩ ምልክቶች አይደሉም፡፡ እናማ… የ‘መምራት’ ትልቁ እሴት… ዲስኩርና በባንዲራ ያሸበረቀ ስብሰባና ‘ሬሴፕሽን’ (ቂ..ቂ…ቂ…) ማብዛት ሳይሆን ‘መሬት ወርዶ’ ሥራ መሥራትና ከሁሉም በላይ ትውልዶችን መንገዶች ላይ የሚኖሩ እንቅፋቶች መቀነስ መሞከር ነው፡፡
የእንቅልፍ ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ስሙኝማ…ሰውየው እልም ያለ እንቅልፍ ወስዶታል፡፡ እናላችሁ…የሆነ ጓደኛው ይመጣና ወዝውዞ ይቀሰቅሰዋል፡፡ ከዛ ምን ይለዋል…“እንቅልፍ ወስዶህ ነበር እንዴ!” ይለዋል፡፡ ይሄኔ ተኝቶ የነበረው በጣም ይናደድና ምን ቢል ጥሩ ነው…“አይ ኮማ ውስጥ ነበርኩ…ህይወቴን ስላተረፍክልኝ አመሰግናለሁ፡፡”
እናማ…ድፍን አገር እንቅልፍ ሲያበዛ ጥሩ ነገር አይደለም፡፡ ‘የማናውቀውን አገር የሚያስናፍቁን’ ነገሮችን ይቀንስልንማ!
በፊት ጊዜ ልጆች ለቡሄ ጊዜ ሲጨፍሩ የሚሏት ስንኝ ነበረች፣
ቡሄ ቡሄ በሉ… ልጆች ሁሉ
የቡሄን አደራ… አንቺ አሞራ
እናላችሁ…“ሀገሬን አደራ…” የምንላት ‘አሞራ’ ነገር ይላክልንማ!
መልካም የበዓል መዳረሻ ሰሞን ይሁንላችሁማ!
ደህና ሰንበቱልኝማ!

Published in ባህል

አብዮቱን ወደ መጠፋፋት ፖለቲካ የወሰደው ኢህአፓ ነው
የብቻ ሩጫ የትም እንደማያደርስ ከነመኢሶን ዘመን ጀምሮ አይተናል
በኢህአፓና በመኢሶን እስረኞች መካከል ልዩነቱ እጅግ በጣም የተካረረ ነበረ

ዶ/ር መረራ ጉዲና “የኢትዮጵያ ፖለቲካ ምስቅልቅል ጉዞና የህይወቴ ትዝታዎች” በሚል ሰሞኑን ለንባብ ባበቁት መጽሐፍ ዙሪያ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ ጋር አጭር ቆይታ አድርገዋል፡፡

መጽሐፉን ያዘጋጁበት ዋና አላማ ምንድነው?
የአሁኑ ትውልድ ስለኛ ትውልድ ያልሆኑ ነገሮችን እየሰማ ነው፡፡ በማይሆን መንገድ የሚነገሩና የሚፃፉ ብዙ ነገሮች ስላሉ እነሱን ለማስተካከልና ለማረም ፈልጌ ነው፡፡ የኔ ትውልድ እና የአሁኑ ትውልድ እንዲግባቡ ለማድረግ የተሞከረበት መጽሐፍ ነው፡፡
በመፅሃፍዎ ላይ መኢሶን ለደርግ ያደረገውን ድጋፍ በተመለከተ፤ “ያን ድጋፍ ባያደርግ ኖሮ ደርግ ተጠናክሮ መውጣት አይችልም ነበር” ብለዋል። በቅርቡ በወጣው የህይወት ተፈራ “ታወር ኢን ዘ ስካይ” መጽሐፍ ደግሞ መኢሶንን በዚህ ድርጊቱ የተነሳ “The bad boy of the Revolution” ብለዋለች፡፡ በዚህ ጉዳይ የእርስዎ አስተያየት ምንድነው?
ሁሉም በየደረጃው ስህተት ሰርቷል፡፡ ጥፋት አጥፍቷል፡፡ በመጽሐፉ ላይ “የኢትዮጵያ ፖለቲካ ቡዳ ማነው” ብያለሁ፡፡ መልሱ እንደመላሹ ይለያያል። እሷ ኢህአፓ ስለነበረች ቡዳው መኢሶን ነው ልትል ትችላለች፡፡ እኛ ደግሞ መኢሶን ስለነበርን ቡዳው ኢህአፓ ነው ልንል እንችላለን፡፡ ነገር ግን የቡዳውን ማንነት ለመመለስ ቀላል አይደለም። መኢሶን የኢህአፓን ጥይት ለመከላከል ይሁን ወይም በሌላ ምክንያት አንድ አመት ከደርግ ጋር በሰራበት ጊዜ በቂ ጥንቃቄ ባለማድረጉ፣ መኢሶንንም ሆነ በአጠቃላይ ትግሉን ጐድቶታል፡፡ ሌላው አብዮት የሚባለውን ነገር ወዳልተፈለገ ፣ ጨርሶ ወደመጠፋፋት ፖለቲካ ይዞ የገባው ከደርግ ቀጥሎ ኢህአፓ ነው፡፡ ለምሳሌ ውይይቱን ወደ ጥይት ለውጦታል፡፡ እስከዛ ድረስ በመኢሶን እና በኢህአፓ መሀል የተወሰኑ ክሮች ነበሩ።
ምን አይነት?
ለምሳሌ እነሀይሌ ፊዳ ከእነ ተስፋዬ ደበሳይ ጋር ይገናኙ ነበር፡፡ ኢህአፓ ፍቅሬ መርዕድን ሲገድል ጨዋታው ፈረሰ፡፡ ሁሉም ነገር እዛ ላይ ቀረ፡፡ ስለዚህ መኢሶን ከደርግ ጋር አብረው እንዲህ አደረጉን የሚለው እንዳለ ሆኖ፣ ኢህአፓ የከተማ ትጥቅ ትግል ብሎ በአብዮቱ ዙሪያ የነበሩ ብዙ ጥያቄዎችን ከቃላት ውይይት ይልቅ ወደ ጥይት ውይይት መውሰዱ ለራሱም ሆነ ለሌላው ቀላል ያልሆነ ጥፋት ነበር፡፡
ሁሉንም ነገር ያበላሸው የጥይት ጉዳይ ነው። ሌሎቹ ስህተቶች የሚታረሙ ነበሩ፡፡ ሰው እንዳይነጋገር፣ እንዳይገናኝ፣ እንዳይመካከር ተደርጐ የመጠፋፋት ጨዋታ ውስጥ ነው የተገባው፡፡ ሌሎች ነገሮች የስትራቴጂ ጉዳዮች ናቸው፡፡ አንዱ ወደ ደርግ ተጠግቷል፤ ሌላው ወደ ኤርትራ ግንባሮች ተጠግቷል የሚሉ ብዙ ክሶች ነበሩ፡፡ በተለይ ግን ምንም በማያውቀው ወጣት ላይ ጦርነት እና ጥይት መከፈቱ በጣም ጐድቶናል፡፡ መጽሐፉ ላይ እንዳየሽው፤ እኛ የሁለተኛ አመት የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ሆነን፣ ራሳችንን በቂ እውቀት እንደሌለን ነበር የምንቆጥረው፡፡ ምክንያቱም የኢህአፓ እና የመኢሶንን ልዩነት አውቆ የገባ ወጣት በጣም የተወሰነ ነው፡፡ እኔ የነበርኩበት ቡድን የሚያነበው አንድ መጽሐፍ ቅዱስ ስለሆነ፣ ያን ለይቶ አቋም መውሰድ ስለተቸገርን ነው ከዘመቻ እስከምንመለስ ድርጅት ውስጥ አንገባም ብለን ወስነን የነበረው። ከዘመቻ ስንመጣ ኢህአፓ ውይይቱን ወደ ጥይት ወስዶት ነበር፡፡ የውስጡንም ቅራኔ በጉልበት ወደ መፍታት ነው የሄደው፡፡ ለዚህ ደግሞ የነጌታቸው ማሩን፣ የእነ ብርሃነ መስቀል ረዳን፣ የነጌታሁን ሲሳይንና የነይርጋ ተሰማን ዕጣ ማየት ነው፡፡
በትግሉ ወቅት የመኢሶን መለያ ምን ነበር?
መኢሶን እኮ ታላቅ ነው፡፡ መንገደኛ አልነበረም። መኢሶንን የፈጠሩ ሰዎች እኮ የትግሉ አንጋፋዎች ናቸው፡፡ ዶ/ር ወርቁ ፈረደ የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ኮሚኒስት ይባል የነበረ ሰው ነው። ከመኢሶን መስራቾች ውስጥ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት በህክምና ወይም በሌላ ዘርፍ ዶክትሬት የነበራቸው ናቸው፡፡ በማንበቡም ሆነ በትምህርት ከነበሩት ሁሉ የተሻሉ ናቸው፡፡ መኢሶኖች ሊከሰሱ የሚችሉት በእድሜ የገፉ፤ መለዘብ ወይም እርጋታ የጀመሩ ናቸው በሚል ነው፡፡ መንገደኞች ግን አልነበሩም፡፡
ቀኝ መንገደኞች የሚባለው ነገርስ?
እሱ ጨዋታ ነው፤ ደርግ ወደኋላ ላይ የለጠፈብን ስም ነው፡፡
የመኢሶንና የኢህአፓ የመጨረሻ ውይይት እንዴት ነበር የተቋጨው?
መኢሶን እና ኢህአፓ የአጭር ጉዞ፣ የረጅም ጉዞ በሚል ሲጨቃጨቁ ከቆዩ በኋላ፣ አፄ ሀይለስላሴ ሊወርዱ ቀናት ሲቀሩ የመጨረሻው ስብሰባ በርሊን ላይ ተደረገ፡፡ ስብሰባው ላይ አልተስማሙም፡፡ አብዮቱ መጥቶ ንጉሱ ሊወርዱ ሲሉም መስማማት አልተቻለም፡፡ ሲለያዩ የኢህአፓው ቡድን፣ የኔን አቋም ትክክለኛነት የካርል ማርክስ እና የሌኒን ሀውልቶች ምስክር ይሆናሉ አለ፡፡ መኢሶን ደግሞ ታሪክ እና የኢትዮጵያ ህዝብ ምስክሬ ነው አለ፡፡ በዚህ ላለመስማማት ተስማምተው ተለያዩ፡፡
በልዩነታቸው በጣም የተበሳጨው ፕሮፌሰር ማሞ ሙጨ፤ እሪ በይ አገሬ ብሎ አለቀሰ፡፡ ሳገኘው እሱን እያነሳሁ እቀልድበታለሁ፡፡ በወቅቱ ቃለ ጉባኤ ፀሐፊው ሀይሌ ፊዳ ነበር፡፡ “የኢህአፓ መሪዎች እንዲህ አሉ -የመኢሶን መሪዎች እንዲህ አሉ … ላለመስማማት ተስማሙ… የሁለቱ መለያየት ያበሳጨው፣ ማሞ ሙጨ ደግሞ በእንባ ለተሰብሳቢው ንግግር አደረገ” ብሎ ጽፏል፡፡ ኢህአፓ ሀውልቱን፣ መኢሶን ታሪክን በምስክርነት ጠርተው ነበር፡፡
ስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲን በተማሪነት ያውቁታል። አሁን ደግሞ በመምህርነት ይመላለሱበታል፡፡ እዚህ ግቢ ውስጥ ካሉ ቦታዎች በትዝታ ወደ ኋላ የሚወስድዎት ምንድነው?
ሁለት ቦታዎች አሉ፡፡ መልሰው መላልሰው ወደዛ ዘመን የሚወስዱኝ፡፡ አንደኛው ልደት አዳራሽ ነው። ብዙ ጊዜ ስብሰባ እናደርግበት ነበር፡፡ በነገራችን ላይ እስካሁን ድረስ ብዙ ውጣ ውረዶችን ያየ አዳራሽ ነው። ኢህአዴግ ሲመጣም ለመጀመሪያ ጊዜ የሰበሰበን እዛ ነው፡፡ ከአፄው ጀምሮ አዳራሹ ታሪካዊ ስለሆነ ወደኋላ ይመልሰኛል፡፡ ሌላው ኪሲንግ ፑሉ ነው፡፡ ከቀልድ ጋር እና ከጥናት እንዲሁም ቆነጃጅቶቻችንንም ከማየት ጋር ተያይዞ ትዝታው ውስጤ አለ፡፡ አሁን ስያሜው ወደ በግ ተራ ተቀይሯል፡፡ አርት ፋካልቲም አንዳንድ ግዜ ስብሰባ እናደርግ ነበር፡፡ ህግ ፋካልቲ ደግሞ የተለየ ዶርም ነበረው፤ እዛ እንሰበሰብ ነበር፡፡ ሁለቱ ግን ዋነኞች ናቸው፡፡ በአፄው ጊዜ መሰብሰቢያ ነበር፤ ደርግም ተጠቅሞበታል፤ ኢህአዴግም በመጀመሪያ ስብሰባውን ያደረገው እዛ ነው፡፡ ኢህአፓና መኢሶን ግጭት ካደረጉባቸው ቦታዎች አንዱ ልደት አዳራሽ ነው፡፡
ብዙ የግድያ ሙከራዎችን አምልጠዋል፡፡ እድል ነው ወይስ …
አጋጣሚዎች ናቸው፡፡ በቀጥታ እኔ ላይ ሊተኮሱ የታሰቡ ጥይቶችን አይደለም የማመልጠው፡፡ ለምሳሌ ኢህአፓና መኢሶን ልደት አዳራሽ የተጋጩ ዕለት ከመኢሶን ውስጥ ሙሉ ስሙን ያልፃፍኩት አጤ፤ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ውስጥ ካለነው የመኢሶን አመራሮች ውስጥ ኢህአፓ አስርጐ ያስገባው ነበር። እሱ የኛን ዝግጅቱ ሙሉ በሙሉ ለኢህአፓ ይንገር አይንገር እግዚአብሔር ይወቀው፡፡ ያ ዝግጅት የከሸፈው አጤ ተነጥሎ ኢህአፓ መሃል ሲገባ ነው። እርምጃ ውሰድ ተብሎ ትዕዛዝ ያልተሰጠው ኢህአፓ፣ “ይሄ ባንዳ መሀላችን ምን ያደርጋል” ብሎ በራሱ ሽጉጥ ጭንቅላቱን መታው፡፡ አንድ አመት ተኩል አካባቢ ሆስፒታል ተኝቷል፡፡ ለምሳሌ ያ ልጅ ባይመታ ኖሮ፣ ኢህአፓ ሊወስድ የተዘጋጀውን እርምጃ አናውቅም። በኋላ ላይ የጠረጠርነው ምንድን ነው … እዚህ ጊቢ ያሉትን ባንዳ የሚባሉትን ሠቅሎ ለመሄድ እንዳሰበ ነው፡፡ ከዛ ከተማ ውስጥ ትንሽ ግርግር ፈጥሮ፣ እነ ኮሎኔል አለማየሁ ሀይሌ ደግሞ ደርግ ውስጥ ያለውን ስራ እንዲሰሩ ነው፡፡ ኢህአፓ ሁሉም ቦታ ከሸፈበት። ገሠሠ በላይ፤ “እዚህ ምንም አንሰራም ራሳችንን እንጠብቅ፤ ከዩኒቨርሲቲ እንውጣ” ብሎኝ ነበር፡፡ እሱን ኢህአፓ ገደለው፡፡ ከሱ ጋር እሺ ብዬ ብሄድ ኖሮ አልተርፍም ነበር፡፡ አምቦ ላይም አማረ ተግባሩ በጠራው ስብሰባ፣ ታላቅ ወንድሜና እነ ዶ/ር ተረፈ ሲገደሉ እኔ በአጋጣሚ ተርፌያለሁ፡፡
ያ ትውልድ ለመስዋዕትነት ዝግጁ የመሆኑን ያህል የመካካድ ባህሉም ስር የሰደደ እንደነበር ወቅቱን ተንተርሰው የሚወጡ ጽሑፎች ያመለክታሉ
መካካዱ እንደዛሬው አይበዛም፡፡ በቁጥር የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ የትግል እምነቱ የጠነከረ ነበር። መካካድ በኢትዮጵያ ታሪክ ስር ሰዶ የቆየ ነው፡፡ ለአላማዬ እሞታለሁ፤ ለአላማም እገድላለሁ የሚለው በወቅቱ ያስቸገረን ጉዳይ ነበር፡፡
በመጽሐፍዎ “ደርግ፤ የመኢሶንን የማሌሪድን፣ የኢህአፓን ልጆች ወረሳቸው” ብለዋል፡፡ ሰው መውረስ ምንድን ነው?
ደርግ ከሁሉም ድርጅቶች ልብሳችሁን ቀይራችሁ ግቡ ብሎ ነበር፡፡ እሱን ነው ውርስ ያልኩት፡፡ ከሱ የተሻለ አማርኛ ስላላገኘሁ ነው፡፡ ቀደም ሲል የሌሎች ድርጅት አባል የነበሩ በኋላ ላይ የደርግ የሆኑትን ለማመልከት ነው፡፡
እስር ቤትም አንድም ቀን አልተገረፉም፡፡ ይሄስ እድል ነው?
እሱን እኮ ተናግሬያለሁ፡፡ ተይዤ ልክ ደርግ ጽ/ቤት በራፍ ላይ ስደርስ አምቦ የማውቀው አወቀ የሚባል ልጅ አገኘሁ፡፡ ምን ያህል እንደረዳኝ ባላውቅም መረራን ረዳሁት ብሎ ለአምቦ ልጆች አውርቷል፡፡
አምቦ ላይ ሲያዙ ገበሬው መንግስቱ ሃይለማርያምን እያሞገሰ በመዝፈኑ ተበሳጭተው እንደነበር ጽፈዋል፡፡ ያው ህዝብ በ97 ምርጫ ላይ በነቂስ ወጥቶ መርጥዎታል፡፡ ነገሩን እንዴት አዩት?
ነገሩ አርሶ አደሮቻችን በነበራቸው ንቃት ላይ ያተኮረ ነው፡፡ ገጠር ውስጥ በደርግ ስር አርሶ አደሩን ማደራጀት ፋሺዝም ነው በማለት፣ ኢህአፓ የመኢሶንን የማንቃት ስራ ይቃወም ነበር፡፡ እኛ ደግሞ ሰፊውን ህዝብ ማደራጀት ፋሺዝም አይደለም እንል ነበር፡፡ በሩቅም ቢሆን እኔን እያወቁ ለሞት አሳልፈው መስጠታቸው የእኔንም እምነት ቀላል ባልሆነ መንገድ እንዲናጋ አድርጓል፡፡ ምን ያህል ሁኔታውን አገናዝበው ነበር የሚለው ሌላ ጉዳይ ነው፡፡ በ1997 ምርጫ ላይ ያኔ ለደርግ አሳልፎ የሰጠኝ የቀበሌ ገበሬ ማህበር ሊቀመንበር ልጅ ነበር የፓርቲያችን ዋነኛ ካድሬ፡፡ እዚህ ላይ ግን ከአርሶ አደር በላይ የኛው የነበሩ የተማሩ ሰዎችም አሳልፈው ሰጥተውናል፡፡
ዛሬ ኢትዮጵያ ውስጥ ላለው ችግር በዋናነት መመለስ ያለባቸው ጥያቄዎች ምንድን ናቸው?
የትግራይ ልሂቃን ስልጣን የሙጥኝ ማለት፣ የአማራ ልሂቃን የኢትዮጵያዊነት ሠርተፊኬት ሰጪ ነኝ ባይነት እና የኦሮሞ ልሂቃን ኦሮሚያን የሚያህል ሰፊ ህዝብ ይዞ የመገንጠልን ሃሳብ ማቀንቀን ናቸው። የትግራይ ልሂቃን ስልጣን ወይም ሞት ማለት፣ ጨዋታው ውሎ አድሮ እነሱንም አይጠቅምም። የአማራ ልሂቃን የኢትዮጵያዊነት ሠርተፊኬት ወይም የበላይነት እኔ ጋ ነው የሚለው ጨዋታም አያዋጣም፡፡ ከሌሎች ጋር ተደራድሮ መሀል መንገድ ላይ ካልተገናኘ የትም መድረስ አይቻልም፡፡ የኦሮሞ ልሂቃን የመገንጠል ጨዋታም የትም አያደርስም። እነዚህ ሶስቱ ነገሮች አቅጣጫ ይዘው በትክክል ካልተፈቱ በስተቀር የኢትዮጵያ ፖለቲካ በኛ ትውልድ የትም ላይደርስ ይችላል፡፡
የሌሎቹ ብሔሮች ቦታስ የት ነው?
መጽሐፉ ላይ አስቀምጫለሁ፡፡ ከዲሞክራሲ ፀጋ ጋር ጠብ የሌላቸውን በተመለከተ ብዙ ዝርዝር ውስጥ አልገባሁም፡፡
ጆሊ ጃኪዝም ለማን የተሰጠ መጠሪያ ነበር?
አሁን የአራዳ ልጆች የምትሏቸው አይነቶች ናቸው፡፡ አውሮፓ እና አሜሪካ ተምረው የመጡ፣ የወቅቱን ፋሽን ይከተሉ የነበሩ ባለ አፍሮ ፀጉሮችና የፖለቲካው ጉዳይ ምንም የማይመስላቸው ነበሩ፡፡
መኢሶን ህቡዕ ሲገባ ስላልነገርዎት ተከፍተው እንደነበርና ከዛም “ፈሪ ለናቱ” የሚል አቋም እንደያዙ መጽሐፉ ውስጥ ጠቅሰዋል፡፡ እስቲ ስለለውጡ ይንገሩኝ---
መኢሶን ህቡዕ ሲገባ ወይም ሲሸፍት ስላልተካተትኩ ተንቄ የቀረሁ መስሎኝ እኔም መሸፈት አለብኝ ብዬ አጥብቄ ተከራክሬ ነበር፡፡ ብሄድ ኖሮ ያው የነሱ ዕጣ ይደርሰኝ ነበር፡፡ ህቡዕ ከገባው ቡድን ውስጥ ለወሬ ነጋሪም የተረፈ የለም፡፡ ሞትን ያመለጥኩበት ሌላው አጋጣሚ ያኔ ነው፡፡ ከዛ በኋላ የመሸፈት ጉጉት ወጣልኝ ማለት ነው፡፡
በየፖለቲካ ፓርቲው የነበረው ልዩነት እስርቤት ድረስ ይዘልቅ ነበር፡፡ እስቲ የእስር ቤቱን ሁኔታ ይንገሩኝ--
ከርቸሌ እየተዋወቅሽ አትነጋገሪም፡፡ በኢህአፓ እና በመኢሶን እስረኞች መካከል ልዩነቱ እጅግ በጣም የተካረረ ነበረ፡፡ በኢህአፓ እና በመኢሶን መሃል ግድግዳ ነበር፡፡
ለኡዝዋ የፀሐፊነት ቦታ የተደረገውን ውድድር በተመለከተ ስለመለስ ዜናዊ ያነሱት ነገር አለ፡፡ እስቲ ስለዚህ ይንገሩኝ…
ኦቦማ የንግግር ችሎታው፣ የቋንቋ ብቃቱ ከፍተኛ ነበር፡፡ በወቅቱ ከነበሩ የኦሮሞ ተማሪዎች የላቀ እውቀት ነበረው፡፡ ለፀሐፊነት የሚወዳደሩት መለስ ዜናዊ እና እሱ ነበሩ፡፡ መለስ ኦባማን እንደማያሸንፍ ስለገባው ከውድድሩ ራሱን አገለለና ኦቦማ አሸነፈ፡፡ ኦቦማ በኋላ ኦነግን ተቀላቅሎ ነበር፤ አሁን በህይወት የለም፡፡ የኢትዮጵያ ታሪክ የሚገርመኝ፣ የሽግግር መንግስት ጊዜ ሌንጮ ለታ ከመለስ ጋር ለፕሬዚዳንትነት ለመወዳደር ከገባ በኋላ ራሱን ከዕጩነት አገለለ፡፡ ይህ የኦሮሞ ህዝብ ትግል ምን አይነት አመራር እንደያዘ ያሳያል፡፡
ወደ አሁኑ ፖለቲካ ስንመጣ…ሰማያዊ ፓርቲ ከሌሎቹ የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር እንደማይሰራ አቋሙን ገልጿል፡፡ ስለፓርቲው አቋም እርስዎ ምን ይላሉ?
እነሱ ወጣቶች ናቸው፡፡ ሮጠው ስላልጠገቡ፣ ሩጫ ገና ስለጀመሩ ነው፡፡ ውለው አድርው ወደ መሀል የሚመጡ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም የብቻ ሩጫ የትም እንደማያደርስ ከነመኢሶን ዘመን ጀምሮ አይተናል፡፡ ሁለት ችግሮች አሉ፤ ስልጣን ለመያዝ ጨዋታው ቀላል አይደለም፡፡ ከተያዘ በኋላም በኢትዮጵያ ሁኔታ አገር ማስተዳደር ቀላል አይደለም፡፡ ለምሳሌ ቱኒዚያና ግብጽን ማየት ይቻላል፡፡ ተቃዋሚዎች ስልጣን ከያዙ በኋላ አገር ማስተዳደሩ ያሰቡትን ያህል ቀላል አልሆነላቸውም፡፡ ግብጽ “ሙባረክ ማረን” እስኪሉ ድረስ እልቂቱ እንደቀጠለ ነው፡፡ ስለዚህ በኛ ትውልድ አንድ ቡድን ይሁንታ አግኝቶ ኢትዮጵያን ይገዛል የሚል እምነት የለኝም፡፡ ኢህአዴግም እዛ ጣጣ ውስጥ ገብቶ ነው መውጣት ያቃተው፡፡ ከኢህአዴግ በላይ ሀይል እና አቅም አግኝቶ የሚንቀሳቀስ ቡድን አላየሁም፤ ነገር ግን ጨዋታው ለኢህአዴግም ከባድ ነው፡፡ ስለዚህ የሰከነ ስራ መስራት እና መተባበር ወሳኝ ነው፡፡ አለበለዚያ
በህልም እና በቅዠት መሞኘት ነው፡፡ ኢህአፓ እና መኢሶን እኮ ቀላል ድርጅቶች አልነበሩም፡፡

ጆሯችንን መርገምት ደፍኖት፣
መርገምቱን ጥይት አቡኖት፣
ጥይቱን አንጠረኛ አድኖት፣
አንጠረኛውን ሙያው ሲያስንቀዉ፣
አእምሮዉን ክፋት ሲያደቀዉ፣
የቦዘኔዎች ምላስ ሲያደርቀዉ፣
አሜሪካዊ ጥቁር ወንድሙም፣ የማንነት
ቀውስ ሲደፍቀው!
አፍሪካዊነት ሲበለጨለጭ፣ ሕሊናችንን
ንዋይ ሲያቅፈው፣
ደናቁርት መሪዎች ታበዩ፤ መደማመጥን
በሀይል ቀፍፈው!
መንግስታት ቡድን አደራጅተው
ፖለቲካቸውንም አስደግፈው፣
ሰውን በሰው ሲያጠፋፉ፣ ከቶ ማን
ይሆን የሚተርፈው!?
የባሩድ ፍንዳታ ያደነቆረው፣
ድንቁርናውን በሌላ ጥይት ፣ እየበሳሳ
የወቀረው...
ወይ እንደ ምንጅላቱ የጠቆረ፣ ወይ
በባንዳነቱ የቀላ፣
የራሱን ጆሮ በሎቲ አስጊጦ፣ የወንድሙን
ግን ያተላ!
ሰዋዊነትም እንስሳነትም፣ እኩል አድኖ
የሚቋደስ፣
የጀግንነት እውቀት ሲያጥረው፣ ግዳይ
ጥሎ የሚፈወስ፣
ለዚህ ሳይሆን አይቀርም፣ አስተሳሰቡ
የደፈረሰው፣
ጀግንነትን እስከ መለኪያው፣ በድንቁርናው
የደቆሰው!
ባሩድ የሚጋት ልሙጥ ጆሮ፣ ሎቲ አንጠልጥሎ
ያየ ሰው፣
‹‹ይኼ ጆሮ አገሩ የት ይሆን?›› ብሎ
ሳይጠይቅ ያድሰው!
ምንም በቀይ ጭንቅላት ጎን፣ በደም
ጨቅይቶ ቢጣበቅም፣
ይኼ ጆሮ እንደሁ አፍሪካዊ ነው፤ ‹የት ነው?›
ተብሎ አይጠየቅም፡፡
የሚንጣጣ ምላሱ እንጂ፣ ግብሩ ማንነቱን
አይደብቅም፡፡
እርግጥ ነው አይደበቅም...!
እንስሳት ማደን ባይቻል፣ የሰው ግዳይ
መቼ ይታጣል፣
ዛሬም ፉከራው ይሰማል፤ የአደን
ጥሪው ይደመጣል፣
በአፍሪካ ‹‹ጀሮ›› ተወዷል፤ በሎቲው
ገና ያጌጣል!
(ለጽንፈኛ አስተሳሰባቸው ሳይሆን፣
የምር ለነጻነት ሲባል ሕይወታቸውን እየከፈሉ ላሉ ግብጻዊያን መታሰቢያ የተገጠመ፣
ነሀሴ 8ቀን 2005ዓ.ም.)

Published in የግጥም ጥግ

እምዬ ሔዋን፣ እምዬ ኢትዮጵያና እምዬ ሉሲ - 3 ወዶ አይሆንም!
የሃይማኖት አክራሪነትን በለዘብተኛ አስተሳሰብ መከላከልና ማሸነፍ የምንችል ይመስለናል። ግን አንችልም። ለሃይማኖት አክራሪነት… ተቃራኒውና ጠላቱ፣ ሁነኛ ማርከሻውና መድሃኒቱ ለዘብተኛነት አይደለም - ፅኑ የሳይንስ ፍቅር እንጂ። ይህንን አለመገንዘባችንም ነው፣ ቁጥር አንድ ድክመታችን። ተስፋ የጣልንበት ለዘብተኛ አስተሳሰባችን፣ እንደምንመኘው አለኝታና ከለላ ሆኖ አያድነንም። በተቃራኒው፣ አክራሪዎች በቀላሉ የሚያጠቁት ስስ ብልት ይሆንብናል። ውሎ አድሮም ለአክራሪዎች እጅ እንድንሰጥ የሚያደርግ የመጀመሪያው ነጥብ እንደሆነ ለማሳየት እሞክራለሁ።
የመሃል ሰፋሪ ወይም የዘብተኛ ሰው ልዩ ምልክት ምን መሰላችሁ? “ሁላችንም ትክክል ነን”… ለማለት የመቸኮሉ ያህል፤ ይሄ አላዋጣ ሲለው… “ሁላችንም ትክክል አይደለንም” ለማለት ይጣደፋል። ለምን በሉ።
ለዘብተኛው መሃል ሰፋሪ፣ ሁሉንም አይነት አስተሳሰብ እያጣቀሰ (ግን ደግሞ ከየትኛውም ሳይሆን) ለመኖር ይመኝ የለ? እናም የመጣውን ሁሉ ተቀብሎ ያስተናግዳል። “እውነት የሚገኘው ከፈጣሪ ቃል ነው፤ የማንኛውም ነገር መመዘኛችንም ሃይማኖታዊ እምነት መሆን አለበት” የሚል ሰባኪ ሲመጣበት፤ … ለዘብተኛው ሰውዬ አእምሮውን ተጠቅሞ ትንሽ ለማሰብና ለማሰላሰል አይሞክርም። “ትክክል ብለሃል” ብሎ በእንብርክክ ስብከቱን ይቀበላል። ብዙ ኢትዮጵያውያን፣ የጥንቱን ስልጣኔ ረስተው ለሺ አመታት በድቅድቅ ጨለማ የዳከሩት፣ በኋላቀርነት መከራ ውስጥ የተዘፈቁት፣ የአክራሪዎች የክርስትና ስብከት በለዘብተኞች ዘንድ ተቀባይነት ስላገኘ ነው። በግብፅ ደግሞ የመሃመድ ሙርሲ ስብከት!
ይሄም ብቻ አይደለም። “እውነት የሚገኘው ከሕዝባዊ ስሜት ነው፤ የማንኛውም ነገር መለኪያችን ሕዝባዊ ስሜትና ነባሩ ባህል መሆን አለበት” የሚል ካድሬ ወይም የሕዝብ ‘ተቆርቋሪ” ሲመጣበትም፤ ለዘብተኛው ሰውዬ አሻፈረኝ አይልም። “አልተሳሳትክም ጓድ! አልተሳሳትክም የወንዜ ልጅ” ብሎ በፓርቲ መፈክር አልያም በባህላዊ ጭፈራ ያስተናግደዋል። በዚህ ሳቢያ ምን እንደተፈጠረ የምታውቁት ይመስለኛል። “ኢትዮጵያ ትቅደም”፤ “ለጭቁኖች የሚወግን ወዛደራዊ አምባገነንነት ይስፈን”፣ “የሰፊው ሕዝብ ድምፅ የፈጣሪ ድምፅ ነው”፤ “ኢትዮጵያ የብሄር ብሄረሰቦች ናት”… በሚሉ መፈክሮችና ጭፈራዎች ብዙዎች ተገርፈው ተረሽነዋል፤ ሚሊዮኖች ተርበው አልቀዋል። በግብፅ ደግሞ፣ የጄነራል አሲሲ የአገር አድን መፈክር!
ለዘብተኛው መሃል ሰፋሪ ግን ይህንን ሁሉ የማመዛዘንና የማገናዘብ ጣጣ ውስጥ መግባት አይጥመውም። የመጣውን ሁሉ ሸክም ችሎ ማደርን ነው የሚፈልገው።
“እውነት የሚገኘው ከሳይንሳዊ ምርመራ ነው፤ የማንኛውም ነገር መለኪያችንና መመዘኛችን ሳይንሳዊ እውቀት መሆን አለበት” የሚል አስተማሪ ወይም ሃኪም ሲመጣስ? በተለመደው ለዘብተኛ አስተሳሰብ፣ …“ትክክል ብለሃል” ብሎ ስክርቢቶና ደብተር ይዞ ለመማር ወይም መድሃኒት ለመውሰድ እጁን ዘርግቶ ይቀበለዋል። እስከ 1900 ዓ.ም ድረስ ከሰላሳ አመት በታች የነበረው የኢትዮጵያውያን አማካይ የሕይወት ዘመን በእጥፍ የጨመረው ለምን ሆነና? አዳሜ፣ ዛሬ ዛሬ በአማካይ 55 ዓመት ገደማ በሕይወት የመኖር እድል አግኝቷል። ከአምስት ሚሊዮን በታች የነበረው የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጥር አሁን 90 ሚሊዮን ለመድረስ የተቃረበውም በሌላ ምክንያት አይደለም። በሳይንስ ነው። በሳይንሳዊ እውቀት አማካኝነት የተገኙ ምርቶች፣ በትምህርት ወይም በእርዳታ መልክ ስለደረሱልን ነው። ለዘብተኛው መሃል ሰፋሪ ግን፣ ዝርዝር መረጃዎችንም ሆነ አንኳር ማስረጃዎችን የመመርመርና አፍረጥርጦ የማሰብ ፍላጎት የለውም።
የለዘብተኛ ብልጠት - ብልሃት መሳይ ሞኝነት
በአንድ ጊዜ ሁሉንም አይነት አስተሳሰብ እያስተናገደ፣ ግን ደግሞ አንዳቸውንም በሙሉ ዓይን ሳይመለከትና ሳይመረምር መኖር ነው የለዘብተኛ ሰው ፍላጎት። ይህንን፣ እንደ ብልህነት ወይም እንደ ብልጣብልጥነት ስለሚቆጥረው ነው፤ “ሁላችንም ትክክል ነን፤ ሁላችሁም ትክክል ናችሁ” ለማለት የሚጣደፈው። በቃ! ሁሉንም የሚያስታርቅ፣ በተለይ ደግሞ አክራሪነትን የሚከላከል ምትሃተኛ ፈውስ ከአንደበቱ ያፈለቀ ይመስለዋል። ሞኝነቱ። ለአክራሪዎች ይሁንታውን በመለገስ፣ ራሱን ለጥቃት አመቻችቶ እያጋለጠ መሆኑን አላወቀም።
አሃ! “ሁላችንም ትክክል ነን” ሲልኮ፣ “እናንተም ትክክል ናችሁ” እያላቸው ነው። ከዚያማ ራሱ በጠረገላቸው መንገድ፣ ራሱ በለገሳቸው ይሁንታ ይገባሉ - “ትክክል መሆናችንን ማመንህ ጥሩ ጅምር ነው” በማለት። ግን በዚያ አያቆሙም። “አንተ ግን ትክክል አይደለህም” ብለው ስለት ይሰነዝሩበታል። “ራስህ እንደመሰከርከው፣ ከሁሉም በፊት ሃይማኖታዊ እምነትን ማስቀደም ያስፈልጋል ማለታችን ትክክል ከሆነ፤ ሌሎች አስተሳሰቦችን ማስቀደም ትክክል ሊሆን አይችልም፤ እውነትን መበረዝና ማርከስ ይሆናላ!” በማለት ለዘብተኛውን አጣብቂኝ ውስጥ ያስገቡታል። “የአገር የቁርጥ ቀን ልጆች ነን፤ የሕዝብ ልሳን ነን” የሚሉ የስሜት ካድሬዎችም በተመሳሳይ ዘዴ ነው ለዘብተኛውን መፈናፈኛ የሚያሳጡት። መሃመድ ሙርሲና ጄነራል አሲሲ በለዘብተኛው የግብፅ ሰው ላይ የሚፈራረቁበት በዚህ መንገድ ነው።
መቆሚያ መቀመጫ ያጣ መሃል ሰፋሪ፣ መውጪያ መግቢያ ያጣ ለዘብተኛ ምን ይዋጠው? ሲጨንቀው፤ “እውነት በሞኖፖል የያዘ የለም፤ ሁላችንም ትክክል አይደለንም፤ ሁላችሁም ትክክል አይደላችሁም” በሚል መከራከሪያ ለማምለጥ ይፍጨረጨራል። ራሱን በራሱ ጠልፎ እየጣለ መሆኑን አላወቀም። “ትክክል አይደለሁም ብለህ መናዘዝህ ጥሩ ጅምር ነው” ይሉታል።
በአጭሩ፤ “ሁላችንም ትክክል ነን” ብሎ ሲናገር፣ ለአክራሪዎችና ለካድሬዎች ይሁንታውን ያበረክትላቸዋል። “ሁላችንም ትክክል አይደለንም” ብሎ ሲናገር ደግሞ፣ በጥፋተኝነት እጁን ይሰጣል። የሙርሲና የአሲሲ መጫወቻ ይሆናል። ለዘብተኛነት አያዋጣም። ከሃይማኖትና ከእምነት በፊት ለሳይንስና ለአእምሮ ቅድሚያ የማንሰጥ ከሆነ፤ ከአክራሪዎች ጋር ተስማምተን ይሁንታችንን ሰጥተን ከእግራቸው ስር ለመንበርከክ እንደተዘጋጀን ይቆጠራል። በመሃል ሰፋሪነት ከዚህና ከዚያ እያጣቀሱ መቀጠል አይቻልም። ለምን? መሰረታዊ የሆኑ ተቃራኒ አስተሳሰቦችን አዳብሎና ቀይጦ መያዝ አያዛልቅማ።
ሁለተኛው የድክመታችን ነጥብ እዚህ ላይ ነው - አክራሪነት፣ ከፖለቲካ ጉዳይነት በእጅጉ የሰፋ መሰረታዊ የአስተሳሰብ ጥያቄ መሆኑን አለመገንዘባችን! መሰረታዊው ግጭት፣ በሳይንሳዊ እውቀት፣ በሃይማኖታዊ እምነት እና በሕዝባዊ ስሜት መካከል ለሺ አመታት የዘለቀ የሶስትዮሽ ግጭት መሆኑን ካላወቅን፣ ለአክራሪዎች እጅ ለመስጠት እንገደዳለን።
ከላይ እንደገለፅኩት፣ ብዙዎቻችን፣ ሶስቱን ተቃራኒ አስተሳሰቦች ቀይጠንና አዋህደን ለማስተናገድ የምንሞክር ለዘብተኞች ነን። ለጊዜው በምሳሌያዊ መጠቆሚያ ልግለፀው። ሃይማኖታዊ እምነትን በመከተል “እምዬ ሔዋን” የሰው ልጆች ሁሉ እናት መሆኗን አምነን እንቀበላለን። ሕዝባዊ ስሜትን በማነፍነፍ፣ “እናት አገር እምዬ ኢትዮጵያ” በሚል ምናባዊ ምስል ተውጠን ሳግ ይተናነቀናል። ሳይንሳዊ ግኝትን በመመርመር ደግሞ፣ “እምዬ ሉሲ” የሰው ዘር ምንጭ እንደሆነች እንገነዘባለን። ከዚያስ?
ከዚያማ፣ እምዬ ሔዋንን፣ እምዬ ኢትዮጵያንና እምዬ ሉሲን አንዳቸውን መምረጥም ሆነ መጣል ሳይኖርብን ጠቅልለንና አዳብለን አልያም ቀይጠንና አዋህደን ለመያዝ መከራችንን እናያለን። እንዲህ ቅይጥ ለዘብተኛ መሆን ብልህነት ይመስለናል። ነገር ግን እምዬ ሔዋን፣ እምዬ ኢትዮጵያና እምዬ ሉሲ አብረው አይሄዱም። ሊቀየጡና ሊዳበሉ አይችሉም።
ሶስቱ ተቃራኒ አስተሳሰቦች፣ አለማችን ላይ በብቸኝነት የበላይነትን ለመቆጣጠር እየተጋጩ፣ በየዘመኑ አንዱ ሌላውን እየገረሰሰና እያንበረከከ ሲነግሱ እንጂ፣ ተቻችለው አብረው ሲኖሩ ወይም ለዘብተኞች ሲያሸንፉ ታይቶ አይታወቅም።

ሃይማኖታዊ እምነት በሳይንስና በሕዝብ ጫንቃ ላይ
ሃይማኖታዊ እምነት በነገሰበት ዘመን፣ የሔዋን ማንነት በስብከት ጎልቶ ይወጣል። ሳይንሳዊ እውቀትና ሉሲ፣ ህዝባዊ ስሜትና እናት አገር ይቀበራሉ፤ አልያም ምድር ቤት ይወረወራሉ፡፡ የክርስትና እምነትን እናስፋፋለን የሚሉ የሃይማኖት ሰባኪዎችና አማኞች ከ1700 አመታት በፊት በአሌክሳንደሪያና በሮም ከተሞች ውስጥ የበላይነትን ሲይዙ ምን ተፈጠረ? ሃይማኖታዊ እምነት በፍፁም ከሳይንሳዊ እውቀትና ከምርምር ግኝት ጋር ተዳብሎ፤ ወይም ከነባር ባህልና ከሕዝባዊ ስሜት ጋር ተቻችሎ አልተቀመጠም።
የአሌክሳንደሪያ የሳይንስና የፍልስፍና ማዕከል ከነ ምሁራኑና ከነ መፃህፍቱ እንዲቃጠል ተደርጓል። ባህላዊ በዓላትና ጭፈራዎች ተወግዘዋል፤ ሃውልቶችና ቅርሶች ፈራርሰዋል፤ ሕዝብ ቢያጉረመርም እንኳ አዋጅ ተጥሎበታል። የሮም እና የሌሎቹም ተመሳሳይ ናቸው። በአሌክሳንደሪያ ከቃጠሎ የተረፉ መፃህፍት እንደገና ከ1300 በፊት እስልምናን እናስፋፋለን በሚሉ ሰዎች ተቃጥለዋል። በቅርቡም እንዲሁ የሙርሲ ደጋፊ አክራሪዎች የአሌክሳንደሪያ ቅርሶችን ኢላማ አድርገዋል። ከቅርባችን የሶማሊያ አልሸባብንም ማየት እንችላለን። ወይም ደግሞ የአፍጋኒስታንን።
ታሊባኖች አፍጋኒስታንን ሲቆጣጠሩ፣ ሴቶች እንዳይማሩ፣ ወንዶች በቴሌቪዥን የመዝናኛ ፕሮግራም እንዳያዩ በመከልከል የሳይንስና የቴክኖሎጂ ጠላትነታቸውን አስመስክረዋል። ነባር አለባበስንና ጭፈራዎችን ለመከልከል፣ ጥንታዊ ቅርሶችን ለማፍረስና ባህላዊ ስርዓቶችን ለማገድ ጊዜ አልፈጀባቸውም። በአንድ ሰማይ ላይ ሁለት ወይም ሦስት ፀሐይ አይኖርም እንዲሉ፣ ሃይማኖት የሚነግሰው ሳይንስንና የምርምር ግኝትን በማንበርከክ፣ እንዲሁም ባህልና የህዝብ ስሜትን በማብረክረክ ነው፡፡

የአክራሪነት ማርከሻ ያገኙ የሳይንስ ጀግኖች
ከጥንቱ የሮምና የአሌክሳንድርያ ታሪክ እስከ ዘመናችን የአልሸባብና የታሊባን ወቅታዊ ዜና… ሁሉም ላይ በግልፅ እንደሚታየው፣ ለዘብተኞች የአክራሪዎችን ዘመቻ ማስቆም አልቻሉም። የሃይማኖት አክራሪነት ሽንፈትን የቀመሰው፣ በለዘብተኞች አማካኝነት ሳይሆን፣ በፅኑ የሳይንስ አፍቃሪዎች ጥረት ነው። ሃይማኖታዊ እምነት ከዙፋን ወርዶ በቦታው ሳይንሳዊ እውቀት የበላይነት ያገኘ ጊዜ ነው፡፡ ያኔ አእምሮ ይከበራል፤ የሉሲ ማንነት በትምህርት እየተዳረሰ ሳይንሳዊ እውቀት ይስፋፋል። ወቅቱ፣ The Age of Reason “የአእምሮ ዘመን”፣ Enlightenment Age “የእውቀት-ፋና ዘመን” ተብሎ ይታወቃል። በዚሁ ወቅት እስከ 19ኛው ክፍለ ዘመን መባቻ ድረስ ሲስፋፋ በቆየው ሳይንሳዊ አስተሳሰብ አማካኝነት አሜሪካ እንዴት እንደተመሰረተች ማየት ይቻላል።
አሜሪካ ውስጥ በ18ኛው ክፍለዘመን አክራሪዎችን ለመቋቋምና ለመከላከል የተቻለው በለዘብተኞች ሳይሆን በሳይንስ አፍቃሪዎች ነው። “ሃይማኖታዊ እምነት ምንም ሆነ ምን፣ በአእምሮና በሳይንስ መመርመር አለበት” በሚሉ ብልሆች ናቸው አሜሪካን የመሰረቷት። እዚህ ላይም በግልፅ የሚታይ ነገር ቢኖር፣ ተቃራኒዎቹ አስተሳሰቦች በጋራ መግዘፍና መንገስ እንደማይችሉ ነው። አእምሮ እና ሳይንስ የሚነግሱት፤ በሃይማኖታዊ እምነትና በህዝባዊ ስሜት ላይ የበላይነትን በመቀዳጀት ነው፡፡
የአሜሪካ መስራቾች ይህንን እውነታ ስለሚያውቁ ነው፤ ከለዘብተኛነት ይልቅ ፅኑ የሳይንስ አፍቃሪ በመሆን ሰፊ ዘመቻ ያካሄዱት፡፡ እምነትንና አእምሮን አቻችለው ለመቀየጥ አልሞከሩም፤ አእምሮን ነው የመረጡት፡፡ ሃይማኖትንና ሳይንስን አስማምተው ለማዳበል አልጣሩም፡፡ ሳይንስን ነው የመረጡት። ለአእምሮና ለሳይንስ ምን ያህል ክብር እንደነበራቸው ለማሳየት ያህል፣ የአንዳንዶቹን አባባል ልጥቀስላችሁ። ቤንጃሚን ፍራንክሊን፣ የእምነትንና የአእምሮን ተቃራኒነት ከመጥቀስ አልፈው፣ ለየትኛው ቅድሚያ እንደሚሰጡ እንዲህ በማለት ገልፀዋል፡ “The way to see by faith is to shut the eye of reason.” በእምነት መመራት፣ የአእምሮን አይን መዝጋት ነው።
የዚያን ዘመን ዝነኛ ፀሃፊ ቶማስ ፔን ደግሞ፣ ሃሳቡን ጠጠር ባለ ቋንቋ ይገልፃል፡ “I do not believe in the creed professed by … any church that I know of. My own mind is my own church.” … “በማናቸውም የሃይማኖት ቤተ መቅደስ ቀኖና አላምንም፤ አእምሮዬ ነው ቤተ መቅደሴ”።
“ሰባኪዎች በሳይንስ ግስጋሴ ይርዳሉ” በማለት የፃፉት ቶማስ ጄፈርሰን በበኩላቸው፣ አክራሪነትን ለመከላከልና በስልጣኔ ጎዳና ለመራመድ ምን ማድረግ እንደሚያስፈለግ ያብራራሉ፡ “Shake off all the fears of servile prejudices, under which weak minds are servilely crouched. Fix reason firmly in her seat, and call on her tribunal for every fact, every opinion. Question with boldness even the existence of a God; because, if there be one, he must more approve of the homage of reason than that of blindfolded fear.
እንዲህ ልተርጉመው፡
“ነፈዞች በታዛዥነት የሚንበረከኩለት የጭፍን እምነት ፍርሃታችሁን ከላያችሁ ላይ አራግፉ። አእምሮን በጠንካራ መሰረት ላይ በማኖር፣ በሁሉም ነገርና በሁሉም ሃሳብ ላይ ዳኝነት እንዲሰጥ አቅርቡለት። የፈጣሪ መኖርና አለመኖርንም ጭምር በድፍረት መርምሩ። ምክንያቱም ፈጣሪ ቢኖር፣ ከጭፍን ፍርሃት ይልቅ የአእምሮ ክብርን እንደሚያስበልጥ አያጠራጥርም…” የቶማስ ጄፈርሰን ንግግር ነው - የአሜሪካ ሶስተኛው ፕሬዚዳንት።
አእምሮውን በፅኑ መሰረት ላይ ያላኖረና ሁሉንም ነገር በአእምሮው የማይመረምር ለዘብተኛ ሰውስ ምን ይጠብቀዋል? መጫወቻ ይሆናላ።
“ሰው፣ አእምሮውን ለሌላ ነገር በምርኮ አሳልፎ የሰጠ ጊዜ፣ ጭራና ቀንዳቸው የማይታወቁና የተቃወሱ የጥፋት ሃሳቦችን የሚከላከልበት መመከቻ አይኖረውም። የአቅጣጫ መቆጣጠሪያ እንደሌለው ጀልባ፣ የነፋስ መጫወቻ ይሆናል” ብለዋል ጄፈርሰን። (Man once surrendering his reason, has no remaining guard against absurdities the most monstrous, and like a ship without rudder, is the sport of every wind.) አንዴ የሙርሲ፣ አንዴ የአሲሲ መጫወቻ ይሆናል!
በአእምሮ እና በሳይንስ ላይ ለዘብተኛ መሆን አያዋጣም ነው ነገሩ። ጄፈርሰን የሳይንስ አፍቃሪ በመሆናቸው፤ እምነትም ሆነ ባህል፣ የሃይማኖት ቀኖናም ሆነ የሕዝብ ስሜት፣ ሁሉም በአእምሮ መመርመርና መመዘን እንዳለበት በመናገር ብቻ አላበቁም። በሃይማኖታዊ መፃህፍት ውስጥ የተካተቱና ሳይንሳዊ እውቀትን የሚቃረኑ “ተአምራት”፣ ፈፅሞ ተቀባይነት ሊኖራቸው አይገባም ብለው በመሰረዝ ቀሪውን በግላቸው ለማሰራጨት ጥረዋል።
እንግዲህ አስተውሉ። የአሜሪካ መስራች አባቶች፣ ከእምነት ይልቅ ለአእምሮ፣ ከሃይማኖት ይልቅ ለሳይንስ ቅድሚያ በመስጠት፣ ጠንካራና የጠራ የአስተሳሰብ መሰረት በመያዝ፣ በዚህም የአክራሪነትን ስረ መሠረት በመናድ ነው ወደ ፖለቲካዊ ጥያቄዎች የተሸጋገሩት።
እነ ጄፈርሰን፣ ከመሰረታዊዎቹ ሶስት ተቃራኒ አስተሳሰቦች መካከል ሳይንሳዊ የእውቀት መንገድን መርጠው በፅናት ስለያዙ፣ ፖለቲካው ብዙ አላስቸገራቸውም። ፖለቲካዊ ጥያቄዎች መልስ የሚያገኙትና መንግስት የሚመሰረተው፣ ከሃይማኖት በፀዳ ሳይንሳዊ መንገድና በአእምሮ እየተፈተሸ መሆን እንዳለበት ገለፁ። አብዛኞቹ የአሜሪካ ሕገመንግስት አርቃቂዎችና አፅዳቂዎች በዚህ ሃሳብ ይስማሙበታል። “The United States of America should have a foundation free from the influence of clergy.” አሜሪካ ከሰባኪዎች ተፅእኖ የፀዳ መሰረት ሊኖራት ይገባል - የአሜሪካ ሁለተኛ ፕሬዚዳንት ጆን አዳም የተናገሩት ነው።
የሃይማኖት ተቋማት በማህበረሰብ ውስጥ ያመጡት ውጤት ምንድነው ለሚለው ጥያቄ ሌላኛው ታዋቂ ፓለቲከኛ ጄምስ ማዲሰን ምላሽ ሲሰጡ፣ “አልፎ አልፎ በሲቪል አስተዳደር መቃብር ላይ መንፈሳዊ አምባገነንነት ሲገነቡ ይታያሉ፤ አብዛኛውን ጊዜ ደግሞ የዘውድ አምባገነንነትን ሲደግፉ ይታያሉ። ለሰው ነፃነት አለኝታ የሆኑበት ጊዜ ግን የለም” በማለት ለዘብተኛ ያልሆነ አቋማቸውን ገልፀዋል … In some instances they have been seen to erect a spiritual tyranny on the ruins of the civil authority; on many instances they have been seen upholding the thrones of political tyranny; in no instance have they been the guardians of the liberties of the people. ከአሜሪካ መስራቾች መካከል አንዱ የሆኑት ጄምስ ማዲሰን የአገሪቱን ህገመንግስት በማርቀቅ ትልቁን ድርሻ የተወጡ ከመሆናቸውም በላይ የአሜሪካ አራተኛ ፕሬዚዳንት ናቸው።
ጆን አዳምስ፣ ቶማስ ጄፈርሰን፣ ጄምስ ማዲሰን እና ሌሎቹ የአሜሪካ ታላላቅ መስራቾች፤ በአለማችን ስር ሰድዶ ለሺ ዘመናት የዘለቀውን አክራሪነት ለመከላከልና ለማሸነፍ የቻሉት፣ በአእምሮና በሳይንስ የበላይነት ላይ ፅኑ አቋም በመያዝ እንጂ በለዘብተኛነት አይደለም።
ይህም ብቻ አይደለም። የሳይንስ አፍቃሪ እንደመሆናቸው፣ ህዝባዊነትንም በፅናት ተቃውመዋል፡፡ አንድ ሃሳብ፣ በብዙ ተከታታይ ትውልዶች በውርስ እየተላለፈ የመጣ ቢሆን እንኳ፣ ትክክለኛ ሃሳብ ላይሆን ይችላል በማለት የባህል የበላይነትን ተቃውመዋል፡፡
የሰዎች ቁጥር፣ የእውነት ማረጋገጫ እንዳልሆነ በመግለፅ የተከራከሩት እነ ጄፈርሰን፣ የእውነት ምንጭ እውኑ ተፈጥሮ እንደሆነ፣ ብያኔ ሰጪው ደግሞ አእምሮ እንደሆነ በግልፅ ተናግረዋል - ሳያለዝቡ። ሕዝባዊ ስሜት የእውነት መመዘኛ አይደለም። ከህዝቡ ውስጥ 99 በመቶ ያህሎቹ፤ ንጉስ እንዲገዛቸውና የፖለቲካ ምርጫ እንዲታገድ ድምፅ ሰጥተውና ተስማምተው ውሳኔ ቢያስተላልፉ እንኳ፣ ውሳኔያቸው ትክክል ይሆናል ማለት አይደለም በማለት ህዝባዊነትን ውድቅ አድርገዋል - እነ ጄፈርሰን፡፡ ለዚህም ነው የአሜሪካ መስራች አባቶች፣ ከህዝብ ስሜት ጋር የማይዋዥቅ፣ በግለሰብ ነፃነት ላይ የተመሰረተ ህገመንግስታዊ ስርዓት ያቋቋሙት፡፡
በአጭሩ ለሳይንሳዊ እውቀትና ለአእምሮ፣ ከሁሉም የላቀ ክብር የሚሰጥ አስተሳሰብ የበላይነት የሚይዘው፣ ስልጣኔና ነፃነት የሚሰፍነው፣ ሃይማኖታዊ እምነትንና ህዝባዊ ስሜትን በማሸነፍ ነው፡፡ እንደገና ለመድገም ያህል፣ ሶስቱ መሠረታዊ የአስተሳሰብ መንገዶች ተቃራኒ ስለሆኑ፣ መሸናነፍና የበላይነት መያዝ እንጂ ተዳብለውና ተቀይጠው መኖር አይችሉም። አሳዛኙ ነገር፣ ከሁሉም በላይ ለሳንሳዊ እውቀትና ለአእምሮ ዋጋ በመስጠት የሚሟገት ምሁር ወይም ፖለቲከኛ በኛ አገር ብዙም የለም። ሦስተኛው የድክመታችን ነጥብ ይሄው ነው።

በሳይንስ ቦታ ሕዝባዊነት፣ በነፃነት ፋንታ ሂትለርና ስታሊን
አገራዊ ባህል እና ሕዝባዊ ስሜት በ20ኛ ክፍለ ዘመን ገንነው የወጡትም በለዘብተኛነት አይደለም። ሳይንስንና አእምሮን ከንግስና በመገልበጥ፣ ሃይማኖትንና እምነትን በመድፈቅ አልያም በማንበርከክ ነው፡፡
“ስዩመ እግዚአብሔር” የሚለው የእምነት ፈሊጥ በመገርሰስ ነው፣ “ኢትዮጵያ ትቅደም” የሚል ሕዝባዊ የፋሺዝም መፈክር የበላይነትን የተቀዳጀው። የብሔር ብሔረሰብ ታርጋ የለጠፉ ሕዝባዊ ቡድኖች ጎልተው የወጡትም በተመሳሳይ መንገድ ነው። የወዛደሩ አምባገንነትን እናሰፍናለን፤ የጭቁኖችን መንግስት እንመሰርታለን የሚሉ ሶሻሊስቶች የነገሱትም፣ በተመሳሳይ መንገድ ሃይማኖታዊ እምነትንና ሳይንሳዊ እውቀትን በማንበርከክ ነው። እናም፣ የሂትለርና የሞሶሎኒ፣ የሌኒንና የስታሊን፣ የማኦ እና የቼጉቬራ ዘመን ተፈጠረ፡፡
የህዝባዊ ስሜት አቀንቃኞች በሃይማኖታዊ እምነት ላይ ብቻ ሳይሆን በሳይንሳዊ እውቀት ላይም ነው የበላይነት የተቀዳጁት፡፡ እንዴት በሉ፡፡ “የራሳችንን ባህል ንቀን የምዕራባዊያንን ሳይንስ ቀድተን መውሰድ የለብንም” ሲባል ሰምታችኋል? የአውሮፓ ሳይንስ፣ የአይሁድ ሳይንስ፣ የኤስያ ሳይንስ፣ የአፍሪካ ሳይንስ… የሚሉ ስያሜዎችን በመለጠፍ ነው፣ እነ ሂትለር የሳይንስን ትርጉም የሸረሸሩት። ሳይንስ በሕዝባዊ ስሜት ስር እንዲንበረከክ ያደረጉት። እነ ሌኒን ደግሞ፣ የቡርዧ ሳይንስና የወዛደር ሳይንስ፣ የበዝባዦች ሳይንስና የጭቁኖች ሳይንስ እያሉ ሳይንስን አራከሱት።
በዚህም ተባለ በዚያ፣ በሦስቱ መሰረታዊ አስተሳሰቦች መካከል መቻቻልና አብሮ መኖር የለም፡፡ ተዳቅሎና ተቀይጦ በጋራ መጓዝ የለም። ከዚያ በኋላ እነማን ቀሩ? የቀረነውማ ቁጥራችን ቢበዛም ከቁጥር የማንገባ ለዘብተኞች ነን። የአቅጣጫ መቆጣጠሪያ እንደሌለው ጀልባ፣ የነፋስ መጫወቻ ነን! ከነፈሰው ጋር መሄድ ብቻ! አንዱን አስተሳሰብ የመመከት ወይም ሌላኛውን አስተሳሰብ የማራመድ አቅም የለንም። ከነፈሰው ጋር እንደገለባ እየተበጠርንና እየተላጋን ለመንጐድ ከፈለግን፤ ለዘብተኛ መሆን “ትክክለኛ” ምርጫ ነው፡፡ በአክራሪነት ማዕበል ተጠራርገን እንዳንሄድ ከፈለግን ግን፣ ለዘብተኛነት አያዋጣም፡፡ የጠራ የነጠረ የሳይንስ አፍቃሪ መሆን ይኖርብናል፡፡

Page 6 of 17