በዓለም የጨርቃጨርቅ ምርት ከፍተኛውን ድርሻ የያዘው የቻይና ገበያ ዋጋ እየተወደደ ስለሆነ ዓለም አቀፍ ገዢዎች ወደ ምሥራቅ አፍሪካ አገሮች እያማተሩ ነው ተባለ፡፡
የሕንድና የአፍሪካን ንግድና ኢንቨስትመንት ለ5 ዓመት ለመደገፍ በዓለም ንግድ ማዕከል የተቋቋመው ፕሮጀክት supporting Indian trade and Investment SITA (ሲታ) ከጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪ ባለሀብቶችና ከሚመለከታቸው የዘርፉ አካላት ጋር በሂልተን ሆቴል ባዘጋጀው የሁለት ቀን የምክክር ወርክሾፕ አለም አቀፍ የጨርቃጨርቅ ገዢዎች  ፊታቸውን ወደ ምስራቅ አፍሪካ አገሮች ማዞር ለኢትዮጵያ ትልቅ አጋጣሚ መሆኑን አመልክቷል፡፡
የወርክሾፑ ዓላማ በሕንድና በአምስት የምሥራቅ አፍሪካ አገሮች (ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ታንዛንያና ሩዋንዳ) መካከል የንግድና ኢንቨስትመንት ትስስር ማሳለጥ እንደሆነ የጠቀሱት የዓለም ንግድ ማዕከል የፕሮጀክት ልማት (ሲታ) አማካሪ ሚስ ሐና ቡሄር፣ ከአንድ ወር በፊት ከጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪ ባለድርሻ አካላት ጋር በዘርፉ ስላሉ ችግሮችና አመቺ ሁኔታዎች ዙሪያ ያደረጉት ምክክር ቀጣይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ሚስ ቡሄር፤ በመጀመሪያም የምክክር ወርክሾፕ የተነሱ ችግሮችና አመቺ ሁኔታዎች ተንትኖ በማዳበር፣ ምርታማነት ተሻሽሎ፣ የሕንድና የዓለም ገበያ በሚፈልጉት መጠንና የጥራት ደረጃ የጨርቃጨርቅ ምርቶችን ማቅረብ የሕንድ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ኢንቨስት የሚያደርጉበትን የተግባር መርሐ ግብር ረቂቅ ይቀረፃል ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ በጨርቃጨርቅ ዘርፍ ለዓለም ገበያ ማበርከት የምትችለው ትልቅ አቅም እንዳላት በመታመኑ ነው በዚህ ዘርፍ እንድትካተት የተደረገው ያሉት ሚስ ቡሄር፣ ሠራተኞች የሙያ ሥልጠና ካገኙ፣ የአመራረትና የማኔጅመንት ሥልጠና ከተሰጠ፣ ብክነት ከተወገደ፣ ዓለም አቀፍ የጥራት ደረጀ ያለው ምርት በአነስተኛ ወጪ ያለማቋረጥ ማቅረብ ከተቻለ…ኢትዮጵያ ከዘርፉ ከፍተኛ ተጠቃሚ እንደምትሆን አስረድተዋል፡፡
ፕሮጀክቱ፣ ለኢትዮጵያ በሥራ ፈጠራ ከሚያስገኝው ጥቅም በተጨማሪ ሥልጠና ይሰጣል፣ የእውቀት ሽግግር እንዴት እንደሚመጣ፣ ዘመናዊ መሳሪያዎችና አዳዲስ ገበያዎች እንዴት ማግኘት እንደሚቻል፣ በአጠቃላይ የቴክኒክ ድጋፍ ያደርጋል እንጂ ገንዘብ እንደማይሰጥ ታውቋል፡፡
የዓለም ንግድ ማዕከል የጥጥ፣ የጨርቃጨርቅና የልብስ ዘርፍ ተፎካካሪነት የፕሮግራም ኦፊሰር ቅድስት ሞገስ ተክሉ በበኩላቸው፤ ቻይና ከምንም (ባዶ) ተነስታ በ30 ዓመት ውስጥ በዘርፉ ከፍተኛ ደረጃ ላይ መድረሷን ጠቅሰው፣ ኢትዮጵያ ጀማሪ አይደለችም፤ አነስተኛ ቢሆንም የጨርቃጨርቅ ምርቶች ኤክስፖርት እያደረገች ነው፡፡ የእውቀትና የቴክኖሎጂ ሽግግር፣ የሙያ ሥልጠናና አስፈላጊ ማሻሻያዎች…ካደረገች በዘርፉ ከፍተኛ ውጤት እንደምታስመዘግብ፣ ገልፀዋል፡፡
በኢትዮጵያ የጉልበትና የኤሌክትሪክ ኃይል ዝቅተኛ መሆን፣ መሠልጠን የሚችል በርካታ የሰው ኃይልና ዋና ዋና ምርት ተቀባይ ገበያ መኖር፣… ኢትዮጵያን በጨርቃ ጨርቅ ምርትና ኢንቨስትመንት የዓለም ሸማቾች ማዕከል ሊያደርጋት እንደሚችል ኦፊሰሯ ገልፀዋል፡፡
ባለፈው ወር ከተደረገው ውይይት እንደተረዳነው፤ ኢትዮጵያን በጨርቃጨርቅ ዘርፍ ለስኬት የሚያበቃት የስትራቴጂ አማራጮች አራት ናቸው ያሉት የዓለም ንግድ ማዕከል የኤክስፖርት ስትራቴጂ ተባባሪ አማካሪ ሚስ አሌክሳንደራ ጐሎ ቮኮ፣ ምርታማነትን ማሻሻልና የሠራተኛውን ክህሎት በማዳበር የምርት ውጤቱን ማሳደግ፣ የዘርፉን ልማት ለማሳደግ አመቺ ሁኔታዎችን መፍጠር፣ ለጨርቃጨርቅ ምርትና ልብስ ዕድገት አንቀሳቃሽ ሞተር የሆኑትን የውጭ ካፒታል ኢንቨስትመንት ማመቻቸትና የምርትና ገበያን ዕድገት በንግድ ኢንፎርሜሽን (መረጃ) መደገፍ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
ሚስ ጐሎቮኮ፣ በዓለም አቀፍ የጨርቃጨርቅና ተጓዳኝ ንግድ፣ ምርትን በዝቅተኛ ዋጋ ማምረት፣ ከቀረጥ ነፃ ዕድል መጠቀም፣ ሸማቾች በሚፈልጉት ፋሽንና ተፎካካሪ በሆነ ዋጋ ምርጥ ምርት ማቅረብ የሚችል አዲስ ተፎካካሪ ትልቅ ዕድል እንዳለው አመልክተዋል፡፡

Saturday, 11 July 2015 12:38

የኪነጥበብ ጥግ

(ስለ ጃዝ ሙዚቃ)
ጃዝ ከሌሎች የሙዚቃ ዘውጎች የተዋሰውን ያህል፣ ለሌሎች የሙዚቃ ዘውጎችም አውሷል፡፡
ኸርቢ ሃንኮክ
የጃዝ ሙዚቃ ገብቶኛል፡፡ አሰራሩንም ተረድቼዋለሁ፡፡ ለዚያም ነው በሁሉም ነገር ላይ የምጠቀምበት፡፡
ቫን ሞሪሰን
 ለውጥ ሁልጊዜ በመከሰት  ላይ ያለ ነገር ነው። የጃዝ ሙዚቃ አንድ ድንቅ ነገር ያ ነው፡፡
ማይናርድ ፈርጉሰን
የጃዝ ሙዚቃ በተፈጥሮው የብዙ የተለያዩ ዓይነት ሙዚቃዎች ጥምረት ነው፡፡
ዴቪድ ሳንቦርን
በቀን ለ3 ሰዓት ያህል ጃዝ አዳምጣለሁ፡፡ ሉዊስ አርምስትሮንግን እወደዋለሁ፡፡
ፊሊፕ ሌቪን
የጃዝ ሙዚቃ እጅግ በርካታ ተዓምረኛ ዝነኞችን ፈጥሯል፡፡
ዊንቶን ማርሳሊስ
ጃዝ ለእኔ ህያው ሙዚቃ ነው፡፡ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ የሰዎችን ስሜት፣ ህልምና ተስፋ ሲገልፅ የኖረ ሙዚቃ ነው፡፡
ዴክስተር ጎርዶን
ጃዝ በጣም ዲሞክራሲያዊ የሙዚቃ ዓይነት ነው፡፡ ከጋራ ተመክሮ ይመነጫል። የየራሳችንን መሳሪያ ይዘን በጋራ ውበትን እንፈጥርበታለን፡፡
ማክስ ሮች
የጃዝ መንፈስ የግልፅነት መንፈስ ነው፡፡
ኸርቢ ሃንኮክ
ጃዝ በሶስት ወይም በአራት ዓመት የምትማረው አሊያም የሙዚቃ ተሰጥኦ ስላለህ ብቻ የምትጫወተው የሙዚቃ ሥልት አይደለም፡፡
ዊንቶን ማርሳሊስ
ጃዝ የመነጨው ከአኗኗር ዘይቤያችን ነው። የአገራችን የጥበብ ዓይነት በመሆኑም ማንነታችንን ለመረዳት ያግዘናል፡፡
ዊንቶን ማርሳሊስ
ጃዝ የግሌ ቋንቋ ነው ማለት እችላለሁ፡፡
ኤሚ ዊኒሃውስ
ጃዝ እንደ ወይን  ጠጅ ነው፡፡ አዲስ ሲሆን ባለሙያዎች፣ ሲቆይ ግን ሁሉም ይፈልገዋል።
ስቲቪ ላሲ

Published in የግጥም ጥግ

በዓለም ትልቁን የእንቁጣጣሽ ፖስት ካርድ በጊነስ ቡክ ለማስመዘገብ ታቅዷል

የዘንድሮው የ“ሀበሻ አዲስ ዓመት ኤክስፖ 2008” ከ15 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደሚደረግበትና ኤግዚቢሽኑን ከቀደምቶቹ የተለየ ለማድረግ ከፍተኛ እንቅስቃሴ በመደረግ ላይ መሆኑ ተገለፀ፡፡
የኤግዚቢሽኑ አዘጋጅ የሀበሻ ዊክሊ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ አደኒክ ወርቁ ሰሞኑን በሀርመኒ ሆቴል ለጋዜጠኞች በተሰጠ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት፤ከዘጠኝ ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ዋጋ ጨረታውን አሸንፈው ማዕከሉን ለአዲስ ዓመት ኤክስፖ የያዙት ሲሆን በኤግዚቢሽኑ ከዚህ ቀደም ያልተለመዱና ለየት ያሉ ፕሮግራሞችን ለማዘጋጀት ጥረት በማድረግ ላይ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ ጨረታውን 50 በመቶ ጭማሪ አድርገው ማሸነፋቸውን የተናገሩት አቶ አዶኒክ፤ በቦታ ሽያጭ ላይ ያደረጉት ጭማሪ ግን ከ7 በመቶ በታች መሆኑንም ገልፀዋል፡፡ በቀን ከ500 ሺህ በላይ ጎብኚ ይኖረዋል ተብሎ በሚጠበቀው የአዲስ ዓመት ኤክስፖ ዝግጅት፣ ከአሁን በፊት ያልተሞከሩና በዓለም ድንቃድንቅ መዝገብ ሊያስመዘግቡ ይችላሉ የተባሉ ነገሮች መዘጋጀታቸውን ጠቁመው፣ ከእነዚህ መካከል በጥንታዊው ብራና የተዘጋጀ በዓለም ትልቁ የእንቁጣጣሽ ፖስት ካርድና የዓለማችን ትልቁ የሻማ ዛፍ እንደሚገኙበት ተናግረዋል፡፡
ከ100 በላይ ድምፃውያን፣ኮሜዲያን እንዲሁም ቀደምትና ዘመናዊ የሀገሪቱ ስመጥር ባንዶች በኤግዚቢሽኑ ላይ እንደሚሳተፉ የተገለጸ ሲሆን ታዋቂውና አንጋፋው ድምፃዊ ጌታቸው ካሣም ሥራዎቹን በኤክስፖው ላይ እንደሚያቀርብ ለማወቅ ተችሏል፡፡ 

 የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በሶርያ ለአመታት የዘለቀውን የእርስ በእርስ ግጭት በመሸሽ ወደተለያዩ አገራት የተሰደዱ የአገሪቱ ዜጎች ቁጥር ከ4 ሚሊዮን በላይ መድረሱንና ይህም ከአገሪቱ ህዝብ አንድ ስድስተኛ ያህሉን እንደሚሸፍን ማስታወቁን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በሶርያ በ2011 የተቀሰቀሰው ግጭት እየተባባሰ መቀጠሉ የአገሪቱን ዜጎች ከፍተኛ ቀውስ ውስጥ እንደከተታቸው የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፉት አራት አመታት በግጭቱ ለህልፈተ ህይወት የተዳረጉ ዜጎች ቁጥር ከ230 ሺህ በላይ መድረሱንና አገራቸውን ጥለው ከተሰደዱት ከ4 ሚሊዮን በላይ ዜጎች በተጨማሪ፣ ከ7 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑትም በአገራቸው ውስጥ መፈናቀላቸውን ገልጧል፡፡
በሶርያ የሚታየውን አስከፊ ሁኔታ፣ “የዚህ ትውልድ አስከፊው የሰብአዊ ቀውስ” ሲሉ የገለጹት የተመድ የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን ሃላፊ አንቶኒዮ ጉቴሬስ፣ የእርስ በእርስ ግጭቱ እያደረሰ ያለው ጥፋት እየከፋ መምጣቱንና ስደቱ በዚሁ ከቀጠለ፣ የስደተኞቹ ቁጥር በመጪዎቹ ስድስት ወራት 4.27 ሚሊዮን ሊደርስ ይችላል ብለዋል፡፡
የተመድ መረጃ እንደሚለው፤ በርካታ ሶርያውያን በተሰደዱባት ቱርክ፣ የስደተኞቹ ቁጥር 1.8 ሚሊዮን የደረሰ ሲሆን፣ በድንበር አካባቢ ያለው ግጭት እየተባባሰ መምጣቱን ተከትሎ የስደተኞቹ ቁጥር እንደሚያሻቅብ ይጠበቃል፡፡ በሊባኖስ 1.2 ሚሊዮን፣ በዮርዳኖስም 629ሺህ ያህል ሶርያውያን ስደተኞች እንደሚገኙ ተመድ አስታውቋል፡፡ በተለያዩ የአውሮፓ አገራት ጥገኝነት የጠየቁ ሶርያውያን ስደተኞች ቁጥር 270 ሺህ ያህል መድረሱንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

ቤትና ንብረቶችን በኢንተርኔት ለመሸጥና ለመግዛት የሚያስችል ዘመናዊ የግብይት ሥራ የሚሰራና ላሙዲ የተባለ አለምአቀፍ የኦንላይን ሪልስቴት ኩባንያ ሥራ ጀመረ፡፡
ደንበኞች ንብረታቸውን በቀላሉ ለመሸጥና ለመግዛት ያስችላቸዋል የተባለውና ዘመናዊው የኢንተርኔት የመገበያያ መንገድ ሥራ መጀመሩን አስመልክቶ ከትናንት በስቲያ በኩባንያው ቢሮ በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ እንደተገለፀው በአገሪቱ የሪል ስቴቶች መስፋፋትና ማደግ ከጊዜ ወደ ጊዜ ለውጥ እያሳየ መጥቷል፡፡ ስለዚህም ደንበኞች ስለሚፈልጓቸው ቤቶችና ንብረቶች በቂና ጥልቀት ያለው መረጃ ለማግኘት የሚችሉበት መንገድ በስፋት ሊኖር ይገባል፡፡
ኩባንያው በገዢና ሻጭ በኦንላይን ተገናኝተው ቤትና ንብረታቸውን ለመገበያየት እንዲችሉ ዕድሉን ያመቻቻል፡፡
ኩባንያው ከዚህ በተጨማሪ ዳያል 4 ሆም የተሰኘ ሆት ላይንን ያስተዋወቀ ሲሆን ይህም ሆትላይን ንብረት ፈላጊዎች ያለ ኢንተርኔት ትስስር ተጠቃሚዎችን በስልክ እንዲገናኙ ለማድረግ የሚያስችል አሠራር ማዘርጋቱንም በዚሁ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተገልጿል፡፡
ላሙዲ በኬንያ፣ በታንዛኒያ፣ በናይጀሪያ፣ በጋና፣ በኡጋንዳና ሩዋንዳ ቢሮዎቹን ከፍቶ እየሠራ የሚገኝ ኩባንያ ነው፡፡   

“ኦባማ አሻፈረኝ ብለው ስለዚህ ጸያፍ ነገር ካወሩ፣ ማዕቀብ እንጥልባቸዋለን!” - የኬንያ ፓርላማ አፈ ጉባኤ
   የኬንያ ከፍተኛ ባለስልጣናት በቅርቡ አገሪቱን ለመጎብኘት ቀጠሮ የያዙትን ባራክ ኦባማን፣ “አደራዎትን በጉብኝትዎ ወቅት የግብረ-ሰዶማውያንን መብት የተመለከተ ነገር እንዳይናገሩ” ሲሉ አበክረው ማስጠንቀቃቸውን ቴሌግራፍ ዘገበ፡፡
የኬንያ ምክትል ፕሬዚደንት ዊሊያም ሩቶና የአገሪቱ ፓርላማ አፈጉባኤ ለኦባማ ባስተላለፉት መልዕክት፣ የግብረ-ሰዶማዊነት ጉዳይ ከክርስትና እምነት ጋር የማይሄድ ጸያፍ ነገር ነውና፣ ሊጎበኙን ሲመጡ ጉዳዩን በተመለከተ ምንም ነገር ትንፍሽ እንዳይሉ ሲሉ አስጠንቅቀዋቸዋል ብሏል ዘገባው፡፡
ከሳምንታት በፊት በመላው ግዛቷ የግብረ-ሰዶማውያንን ጋብቻ በህግ የፈቀደችውን አሜሪካን የሚመሩት ኦባማ ግን፣  ከዚህ ቀደምም ደቡብ አፍሪካ፣ ታንዛኒያ እና ሴኔጋልን ሲጎበኙ እንዲህ ያለ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸው፣ አሻፈረኝ ብለው ስለ ግብረ-ሰዶማውያን መብቶች በአደባባይ እንዳወሩት ሁሉ፣ የኬንያን ባለስልጣናት ማስጠንቀቂያንም ጆሮ ዳባ ልበስ ሊሉት ይችላሉ ተብሏል፡፡
ባለፈው እሁድ ናይሮቢ ውስጥ በሚገኝ አንድ ቤተክርስቲያን በተካሄደ ስነስርዓት ላይ፣ በርካታ ምዕመናን ለግብረ-ሰዶማዊነት ያላቸውን ተቃውሞ የገለጹ ሲሆን፣ ኦባማ እና ኦባማ ወይም ሚሼል እና ሚሼል እንዲመጡ አንፈልግም ሲሉ የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻን ነቅፈዋል፡፡
በስፍራው የተገኙት ምክትል ፕሬዚዳንቱ ሩቶም፣ የምዕመናኑን ተቃውሞ በመደገፍ፣ እንዲመጡልን የምንፈልገው ኦባማ እና ሚሼልን ነው፤ ልጅ እንዲወለድልንም እንፈልጋለን ሲሉ በመናገር፣ አገራቸውን ከእንዲህ ያለው ጸያፍ ሃሳብ እንደሚከላከሉ ለምዕመናኑ ቃል ገብተዋል፡፡
የኬንያ ፓርላማ አፈ ጉባኤ ጀስቲን ሙቱሪ በበኩላቸው፣ አገራቸውና ህዝባቸው ጸያፍ ነገሮችን እንደማይፈልጉ በመግለጽ፣ ኦባማ ወደ አገራችን ከገቡ በኋላ የግብረ-ሰዶማውያንን መብቶች በተመለከተ ንግግር እንዳያደርጉ እናግዳቸዋለን፣ አሻፈረኝ ብለው ከተናገሩም ማዕቀብ እንጥልባቸዋለን ሲሉ ተናግረዋል፡፡   
ኦባማ ከሁለት ሳምንታት በኋላ የአባታቸው እትብት የተቀበረባትን ኬንያን ይጎበኛሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

የዘመድ ችግር የሚፈታው በዘመድ ነው፡፡
የስዋሃሊ አባባል
በጋራ ጀልባ ወንዙን ተሻገሩ፡፡
የቻይናውያን አባባል
እዩኝ እዩኝ ማለት ለትችት ያጋልጣል፡፡
የጃፓናውያን አባባል
ማስታወቂያ የንግድ እናት ነች፡፡
የጃፓናውያን አባባል
ልብ ትክክል ሲሆን ስራም ትክክል ይሆናል፡፡
የጃፓናውያን አባባል
ብዙ የምታስካካ ዶሮ ብዙ እንቁላል አትጥልም፡፡
የኮሪያውያን አባባል
የዛፍ ፍሬ ከዛፉ ርቆ አይወድቅም፡፡
የኮሪያውያን አባባል
በእጅህ መዳፍ መላውን ሰማይ ልሸፍን አትበል፡፡
የኮሪያውያን አባባል
ብዙ እጆች የሥራ ጫናን ያቀላሉ፡፡
የሰሜን አሜሪካውያን አባባል
አንድ ግንዲላ ብቻውን ምድጃ እንኳን ለማሞቅ በቂ አይደለም፡፡
የእስያውያን አባባል
መቶ ሰዎችን ለማስፈራራት አንዱን ግደል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ውሃ ጀልባን ማንሳፈፍ ብቻ ሳይሆን ማስመጥም ይችላል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ባዶ ጆንያ ቀጥ ብሎ መቆም አይችልም፡፡
የስዋሂሊ አባባል
አንድ ምሰሶ ቤት አያቆምም፡፡
የስዋሂሊ አባባል
ብዙ ካፒቴኖች ያሏት መርከብ መስጠሟ አይቀርም፡፡
የስዋሂሊ አባባል
ሁለት እርምጃ መንገድ አይሆንም፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል
ወላጆችህ ጥርስህን እስከምትነቅል ከተንከባከቡህ፣ አንተም ጥርሳቸውን እስኪ ነቅሉ ትንከባከባቸዋለህ፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል

Published in ከአለም ዙሪያ

 7ሺህ 800 ሰራተኞቹን ለመቀነስ ወስኗል

    ታዋቂው ማይክሮሶፍት ኩባንያ በኖኪያ የስማርት ሞባይል ቀፎ ንግዱ ላይ 7 ነጥብ ስድስት ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ ማጋጠሙን ተከትሎ፣ 7ሺህ 800 ሰራተኞችን ከስራ ገበታቸው እንደሚቀንስ ባለፈው ረቡዕ ማስታወቁን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡
ከሁለት አመታት በፊት ኖኪያን በ7.3 ቢሊዮን ዶላር የገዛውና የሞባይል ቀፎዎችን እያመረተ ለገበያ ማቅረብ የጀመረው ማይክሮሶፍት፣ ቢዝነሱ አላዋጣው ማለቱን በማየት ባለፈው አመት ብቻ 12 ሺህ 500 ሰራተኞቹን እንደቀነሰ ያስታወሰው ዘገባው፣
ማይክሮሶፍት ከለመደው የኮምፒውተር ዘርፍ ወጣ ብሎ የተሰማራበት የሞባይል ቀፎ ንግድ ኪሳራ ላይ ጥሎታል ያሉት የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ሳትያ ናዴላ፣ ቢዝነሱ ለምን አክሳሪ እንደሆነና በቀጣይ መወሰድ የሚገባቸውን እርምጃዎች በተመለከተ ግምገማ እያደረግን ነው ብለዋል፡፡
ኩባንያው በቅርቡ የስማርት ፎን ንግዱን አዋጭ በሆነ ሁኔታ ማስቀጠል የሚችልበትን አዲስ አቅጣጫ እንደሚዘረጋና 18ሺህ ሰራተኞቹን መቀነስን ጨምሮ ሰፊ የመዋቅር ለውጥ እያደረገ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡
ማይክሮሶፍት የፊንላንዱን ኖክያ የገዛው፣ ከዚህ በፊት ያመርታቸው የነበሩትን የዊንዶውስ ሞባይሎች ከአፕል አይፎኖችና ከጎግል አንድሮይድ ሲስተሞች ጋር በገበያ ላይ ተወዳዳሪ ለማድረግ በማሰብ እንደሆነም ዘገባው ጨምሮ አስታውሷል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

      በአውሮፓ እግር ኳስ የተጨዋቾች የዝውውር መስኮት ከተከፈተ ሁለት ሳምንታት ተቆጥረዋል፡፡ ዘንድሮ የዝውውር መስኮቱ ከተግባራዊ ግብይት ውጭ በገበያው አነጋጋሪ ሆነው በሰነበቱ ወሬዎች  የተሞላ መስሏል። ከተጨዋቾች ሰርጂዮ ራሞስ፤ አርዳም ቱራም፤ ራሂም ስተርሊንግ እና ፖል ፖግባ የዝውውር ገበያው አበይት ወሬ ሆነው ሰነባብተዋል፡፡ ከክለቦች በአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር የተጨዋቾች የዝውውር ህገ ደንብ ተቀጥተው የነበሩት ፓሪስ ሴንትዠርመን፤ ቼልሲ እና ባርሴሎና ወደ ገበያው መመለሳቸው ሲያነጋግር እንደ ሊቨርፑል አይነት ክለቦች ደግሞ ከበርካታ የዝውውር ወሬዎች ጋር ስማቸው ሲነሳ አሳልፈዋል፡፡  በሌላ በኩል የጣሊያን ሴሪ ኤ ክለቦች ወደ ዝውውር ገበያው በንቁ ተሳትፎ መግባታቸው ሰፊ ሽፋን እያገኘ ነው፡፡ ከ2 ሳምንት በፊት የተጀመረው የዝውውር ገበያው ከ48 ቀናት በኋላ የሚዘጋ ይሆናል፡፡
የስፔኖቹ ሪያል ማድሪድ እና ባርሴሎና፤ የእንግሊዞቹ የማንችስተር ከተማ ክለቦች እና ቼልሲ እንዲሁም የፈረንሳዩ ፓሪስ ሴንትዥርመን ባለፉት የውድድር ዘመናት በዝውውር ገበያው ያደርጉት የነበረው ንቁ ተሳትፎ ዘንድሮ የቀዘቀዘ ይመስላል፡፡ በዘንድሮ ገበያ ግን ባልተለመደ ሁኔታ ትልልቅ ተጨዋቾችን እያሳደዱ እያስፈረሙ የሚገኙት የጣሊያን ክለቦች ሆነዋል። በተለይ ባለፈው የውድድር ዘመን በሴሪኤው እስከ 3 ያለውን ደረጃ ይዘው ያጠናቀቁት ጁቬንትስ፤ ኢንተርሚላንና ሮማ በገበያው እያንዳንዳቸው ከ3 ተጨዋቾች በላይ በመግዛት ተጠናክረዋል፡፡ የጣሊያን ክለቦች ቢያንስ ላለፉት 5 የውድድር ዘመናት በብድር፤ ያለዝውውር ዋጋ በሚለቁ ተጨዋቾች እና በአውሮፓ ደረጃ በቀነሰ የፉክክር ደረጃቸው ተዳክመው ነበር፡፡ ዘንድሮ ግን ባለፈው ዓመት ለሻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ በመድረስ ጁቬንትስ ባገኘው ስኬት በመነቃቃት ላይ ናቸው፡፡ አዳዲስ ባለሃብቶች  በጣሊያን ክለቦች ላይ ፍላጎት በማሳደር ኢንቨስትመንታቸውን ማጠናከራቸው ገና ከጅምሩ ለውጥ በመፍጠር ላይ ነው፡፡ በወቅቱ የዝውውር ገበያ የሴሪኤ ክለቦች በሁለት ሳምንታት ውስጥ እስከ 262 ሚሊዮን ዩሮ አውጥተዋል፡፡
በተያያዘ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር በሁለቱ ክለቦች ማን ሲቲ እና ፒኤስጂ የተጨዋቾች የዝውውር ወጪ እና የቡድን ስፋት የጣለውን ገደብ ማንሳቱ አበይት መነጋገርያ እየሆነ መጥቷል፡፡ ማንችስተር  ሲቲ በአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር በተጣለበት እግድ በሻምፒዮንስ ሊግ በ21 ተጨዋች እንዲሳተፍ እና ወጪው ከፍተኛው በ45 ሚሊዮን ዩሮ እንዲገደብ ተወስኖ ለሶስት የውድድር ዘመን 49 ሚሊዮን ፓውንድ ተቀጥቶ ነበር፡፡ በአውሮፓ የእግር ኳስ ማህበር አማካኝነት በፋይናንስ ጨዋነት ደንብ ባለፉት አራት የውድድር ዘመናት ተግባራዊ በመሆኑ የአህጉሪቱ ትልልቅ ክለቦች እዳ ከ1.7 ቢሊዮን ዩሮ ወደ 487 ሚሊዮን ዩሮ ሊወርድ ችሏል፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ደንቡን ተግባራዊ በማድረግ በተለይ ባለፉት ሁለት ዓመታት ከ23 ክለቦች ጋር በተለይ ሲቲ፤ ፒኤስጂ ፤ ኢንተርሚን እና ከመሳሰሉት ጋር በቅርበት ይሰራ ነበር፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ሰሞኑን ይህን መመርያ መጠነኛ መሻሻል አድርጎበት ለሚቀጥሉት ሶስት የውድድር ዘመናት ክለቦች አጠቃላይ ኪሳራቸው ከ45 ወደ 30 ሚሊዮን ዩሮ እንዲወርድ አድርጓል፡፡በአምስቱ ታላቅ ሊጎች የሚወዳደሩ 98 ክለቦች ባለፈው የውድድር ዘመን በተካሄዱ የዝውውውር ገበያዎች በድምሩ እስከ 8.6 ቢሊዮን ዩሮ ያወጡ ሲሆን ይህም በአንድ ክለብ አማካይ 87.7 ሚሊዮን ዩሮ ይሆናል፡፡
ከእንግሊዝ ክለቦች በዝውውር ገበያው ንቁ ተሳትፎ በማድረጉ ግንባር ቀደም ተጠቃሽ የሚሆነው እስካሁን አምስት ተጨዋቾች ያስፈረመው ሊቨርፑል ነው። በተለይ ብራዚላዊው ሮበርቶ ፊርሚኖ ያዛወረበት የ41 ሚሊዮን ዩሮ ሂሳብ የፕሪሚዬር ሊጉ ትልቁ ክፍያ ሲሆን እውቁን የክለቡ አምበል ስቴቨን ጄራርድ ወደ አሜሪካ ያሰናበተበት ሁኔታ አበይት ትኩረት የሳበ ነበር፡፡ ስተርሊንግ የዝውውር ገበያው አበይት መነጋገርያ ሊሆን የበቃ ነው፡፡ ተጨዋቹ ከክለቡ ሊቨርፑል እንደሚለቅ መወራት ከጀመረ ሁለት ወራት ተቆጥረዋል፡፡ ማን ሲቲ ዋና ፈላጊው ሲሆን በመጀመርያ 25 ከዚያ 30 እንደገና 35 ሚሊዮን ዩሮ ሂሳብ በማቅረብ ሊያዛውረው ቢታገልም አልተሳካለትም፡፡ ሲቲ አሁን የዝውውር ሂሳቡን ከሌሎች ጥቅማ ጥቅሞች ጋር ወደ 40 ሚሊዮን ፓውንድ አሳድጎታል፡፡
አርሰናል ባልተገለፀ የዝውውር ሂሳብ ከቼልሲ ፒተር ቼክን ማዛወሩና ሉካስ ፖዶልስኪ ለፌነርባቼ መሸጡን ጨምሮ አምስት ተጨዋቾች ማሰናበቱ፤ ራዳሜል ፋልካኦን በውሰት ከሞናኮ አስመጥቶ ድሮግባ እና ፒተር ቼክን ጨምሮ አምስት ተጨዋቾችን የለቀቀው ቼልሲ፤  ማንሲቲ በግብይቱ ከመወራቱ በቀር የጎላ ዝውውር አለማድረጉ፤ ማን ዩናይትድ ከሆላንዱ ፔኤስቪ ሜምፊስ ዴምባይን በ30 ሚሊዮን ዩሮ በማዛወር የፈፀመው ግብይት ዋናዋናዎቹ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ የዝውውር ክንውኖች ናቸው፡፡ በሌሎች የአውሮፓ ሊጎች ባለፉት 15 ቀናት ከተፈፀሙ ግብየቶች ዳኒሎ በ23 ሚሊዮን ፓውንድ ከፖርቶ ወደ ሪያል ማድሪድ፤ ዣቪ ከባርሴሎና በነፃ ዝውውር ወደ አልሳድ፤ ሳሚ ከዲራ ከሪያል ማድሪድ ወደ ጁቬንቱስ በነፃ፤ ካርሎዝ ቴቬዝ ከጁቬንትስ ወደ አርጀንቲናው ክለብ ቦካ ጁኒዬርስ በነፃ እንዲሁም አንድሬ ፒርሎ ከጁቬንትስ ወደ አሜሪካው ኒውዮርክ ሲቲ በነፃ ያደረጓቸው ዝውውሮችም ይጠቀሳሉ፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ ምርጥ ግዢ የሚባለው ከ20 ሚሊዮን ዩሮ በላይ የዝውውር ሂሳብ የሚከፈልበት ግብይት ነው፡፡በሊቨርፑልና በአርሰናል ክፉኛ ቢፈለግም ከፖርቱጋሉ ኤፍሲ ፖርቶ ወደ አትሌቲኮ ማድሪድ በ35 ሚሊዮን ዩሮ የተዛወረው ጃክሰን ማርቲኔዝ ፤ ከአትሌቲኮ ማድሪድ ወደ ጣሊያኑ ጁቬንትስ በ19 ሚሊዮን ዩሮ ሂሳብ የገባው ማርዮ ማንዱዚክ፤ ከፈረንሳዩ ክለብ ማርሴይ ወደ ኤፍሲ ፖርቶ የዞረው ጂያኔሊ ላምቡላ፤ ከፈረንሳዩ ሞናኮ ወደ ኢንተርሚላን በ35 ሚሊዮ የተሻገረው ጄዮፍሪ ኮንዶጊባ፤ ከጀርመኑ ክለብ ባየር ሌቨርኩዘን ወደ ሌላው የጀርመን ክለብ ቦርስያ ዶርትመንድ የሄደው ጎንዛሎ ካስትሮ ምርጥ ዝውውሮች ተብለዋል፡፡
ትራንስፈርማርከት ተቀማጭነቱን በጀርመን አድርጎ በስምንት የአውሮፓ አገራት ቋንቋዎች የሚሰራጭ እና ከተመሰረተ 15 ዓመታት ያስቆጠረ ድረገፅ ነው፡፡ ድረገፁ ስለ ዓለም እግር ኳስ የተለያዩ የውጤት መረጃዎች፤ ጥቆማዎች እና ዜናዎች እንዲሁም የዝውውር ገበያ ምልከታቸውን በይዘቱ ያካትታል። ትራንስፈርማርኬት የተጨዋቾች የዝውውር ገበያን በመላው ዓለም በመከታተል በሚያደርጋቸው ጥጭናቶች የሚያቀርባቸው ግምታዊ ስሌቶች እና የገበያ ግምገማዎች በትክክለኛነታቸው ከፍተኛ ተዓማኒነት አትርፈውለታል።
በ5ቱ ታላላቅ ሊጎች የተጨዋቾች ዋጋ ተመንና የመጤዎች ብዛት
ከዚህ በታች የቀረበው የአውሮፓ 5 ታላላቅ ሊጎች ውስጥ በሚወዳደሩ ክለቦች የሚገኙ ተጨዋቾች ብዛት ፤ አጠቃላይ የዋጋ ተመን እንዲሁም ከተለያዩ አገራት በየሊጎቹ የሚጫወቱ መጤ ፕሮፌሽናሎችን ብዛት ይጠቁማል፡፡
የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ 20 ክለቦች፤ 551 ተጨዋቾች፤ 3.8 ቢ.ዩሮ፤ 375 መጤ ተጨዋቾች
የስፔን ፕሪሚዬራ ሊጋ 20 ክለቦች፤ 551 ተጨዋቾች፤ 3.8 ቢ.ዩሮ፤ 168 መጤ ተጨዋቾች
የጣሊያን ሴሪኤ 20 ክለቦች፤ 592 ተጨዋቾች፤ 2.42  ቢ.ዩሮ፤ 304 መጤ ተጨዋቾች
የፈረንሳይ ሊግ 1 20 ክለቦች፤ 527 ተጨዋቾች፤ 1.38 ቢ.ዩሮ፤ 237 መጤ ተጨዋቾች
የጀርመን ቦንደስ ሊጋ 18 ክለቦች፤ 513 ተጨዋቾች፤ 2.34 ቢ.ዩሮ፤ 246 መጤ ተጨዋቾች
አዳዲስ ዋጋ የወጣላቸው
የወቅቱ የዝውውር ገበያ ያወጣቸው እና አዳዲስ ዋጋ የወጣላቸው 5 ተጨዋቾች ከዚህ በታች የቀረቡት ናቸው። ተጨዋቾቹ በአመዛኙ የደቡብ አሜሪካ አገራትን የወከሉ እና በቅርቡ ተካሂዶ ከነበረው ኮፓ አሜሪካ ጋር በተያያዘ ትኩረት ያገኙ ናቸው፡፡ ከመካከላቸው አንድ የአልጄርያ ዜግነት ያላው ተጨዋችም አለ፡፡ ደቡብ አሜሪካዊያኑ  ተጨዋቾች በሁለቱ የፖርቱጋል ክለቦች ቤነፊካ እና ኤፍሲ ፖርቶ የሚጫወቱ ናቸው፡፡ የተጨዋቾቹ ሙሉ ስም፤ የሚጫወቱበት ስፍራ፤ ዜግነታቸው፤ እድሜያቸው፤ ክለባቸው እና የዋጋ ተመናቸው በቅድመ ተከተል እንደቀረበው ነው፡፡
ኒኮላስ ጋይቴን ፤ ግራ ክንፍ ፤አርጀንቲናዊ፤ እድሜ 27 ፤ቤነፊካ፤ 27 ሚሊዮን ዩሮ
ዊልያም ካርቫልሆ፤ የመሃል ተከላካይ፤ ፖርቱጋላዊ፤ እድሜ 23 ፤ስፖርቲንግ ሊዝበን ፤ 26 ሚሊዮን ዩሮ
ቶቶ ሳልቪዮ፤ ቀኝ ክንፍ ፤ አርጀንቲናዊ ፤እድሜ 24 ፤ቤነፊካ ፤22 ሚሊዮን ዩሮ
አሌክስ ሳንድሮ ፤ግራ ተመላላሽ ፤ብራዚላዊ፤ እድሜ 24 ፤ኤፍሲ ፖርቶ፤ 20 ሚሊዮን ዩሮ
ያሲኒ ኢብራሂሚ ፤ግራ ተመላላሽ፤ አልጄርያዊ ፤እድሜ 25፤ኤፍሲ ፖርቶ፤ 18.5 ሚሊዮን ዩሮ
ዋጋቸው የጨመረላቸው
ከዚህ በታች የቀረቡት አምስት ተጨዋቾች በዝውውር ገበያው አስቀድሞ ከነበራቸው ዋጋ ጭማሪ ያሳዩ ናቸው። ከመጀመርያዎቹ አራት ተጨዋቾች  ሶስቱ በስፔኑ ሪያል ማድሪድ፤ አንዱ በባርሴሎና የሚገኙ ናቸው፡፡
አንጄል ዲማርያ ፤ቀኝ ክንፍ ፤አርጀንቲናዊ፤ እድሜ 27 ፤ያሳየው የዋጋ ጭማሪ 116.7 በመቶ ፤የወቅቱ ዋጋ 65 ሚሊዮን ዩሮ
ጄምስ ሮድሪጌዝ ፤የአጥቂ አማካይ ፤ኮሎምቢያዊ፤ እድሜ 23 ፤ያሳየው የዋጋ ጭማሪ 71.4 በመቶ ፤የወቅቱ ዋጋ 60 ሚሊዮን ዩሮ
ክርስትያኖ ሮናልዶ፤ ግራ ክንፍ፤ እድሜ 30፤ ያሳየው የዋጋ ጭማሪ 20 በመቶ ፤የወቅቱ ዋጋ 120 ሚሊዮን ዩሮ
ኔይማር፤ ግራ ክንፍ፤ ብራዚላዊ፤ እድሜ 23፤ ያሳየው የዋጋ ጭማሪ 33.3 በመቶ፤ የወቅቱ ዋጋ 80 ሚሊዮን ዩሮ
ኮኬ፤ ግራ ክንፍ፤ ብራዚላዊ፤ እድሜ 23፤ ያሳየው የዋጋ ጭማሪ 66.7 በመቶ፤ የወቅቱ ዋጋ 50 ሚሊዮን ዩሮ
ዋጋቸው የወረደባቸው
በእድሜያቸው መግፋት፤ በብቃታቸው መውረድ እና ተፈላጊነታቸው እየቀነሱ በመምጣቱ ትልልቅ ተጨዋቾች ዋጋቸው እየወረደ መጥቷል፡፡ በዘንድሮ የተጨዋቾች የዝዝዝውር ገበያ አስቀድሞ ከነበራቸው ዋጋ የቀነሰባቸው 5 ተጨዋቾች የሚከተሉት ናቸው፡፡
አንድሬስ ኢንዬስታ የመሃል አማካይ፤ ስፔናዊ፤ እድሜ 37፤ በ20 ሚሊዮን ዩሮ ዋጋው ቀንሶ የወቅቱ ግምቱ 35 ሚሊዮን ዩሮ
ኤዲሰን ካቫኒ የመሃል አጥቂ፤ ኮሎምቢያዊ፤ እድሜ 28፤ በ18 ሚሊዮን ዩሮ ዋጋው ቀንሶ የወቅቱ ግምቱ 42 ሚሊዮን ዩሮ
ሮቢን ቫንፒርሲ የፊት አጥቂ፤ ሆላንዳዊ፤ እድሜ 31፤ በ15ሚሊዮን ዩሮ ዋጋው ቀንሶ የወቅቱ ግምቱ 25 ሚሊዮን ዩሮ
ራዳሜል ፋልካኦ የፊት አጥቂ፤ ኮሎምቢያዊ ፤እድሜ 29፤ በ15ሚሊዮን ዩሮ ዋጋው ቀንሶ የወቅቱ ግምቱ 45 ሚሊዮን ዩሮ
ማርዮ ባላቶሊ የፊት አጥቂ፤ ጣሊያናዊ፤ እድሜ 24፤ በ15 ሚሊዮን ዩሮ ዋጋው ቀንሶ የወቅቱ ግምቱ 15 ሚሊዮን ዩሮ
ከአምስቱ ተጨዋቾች ሌላ  በገበያው ዋጋቸው የወረደባቸው ሌሎቹ ተጨዋቾች  ዝላታን ኢብራሞቪች ከ28 ወደ 15 ሚሊዮን ዩሮ፤ ሽዋንስታይገር ከ40 ወደ 28 ሚሊዮን ዩሮ፤ ቶሬስ ከ19 ሚሊዮን ወደ 7 ሚሊዮን ዩሮ፤ ላሳና ዲያራ ከ16 ወደ 4 ሚሊዮን እንዲሁም ሉካስ ፖዶልስኪ ከ33 ወደ 12 ሚሊዮን ዩሮ ተመናቸው አሽቆልቁሏል፡፡
ከፍተኛ የዝውውር ዋጋዎች
በትራንስፈር ማርኬት ድረገፅ  በዓለም እግር ኳስ የተመዘገቡ ከፍተኛ የዝውውር ዋጋዎችን በሶስት ዘርፎች መድቦ መክፈል ይቻላል፡፡ 120 ሚሊዮን ዩሮ የተተመኑት ሁለት ተጨዋቾች ሊዮኔል ሜሲ እና ክርስትያኖ ሮናልዶ ናቸው፡፡ በሚሊዮን ዩሮ ዋጋቸው የተተመነላቸው  አራት ተጨዋቾች ጀምስ ሮድሪጌዝ፤ ኔይማር ጋሬዝ ባሌ ሲሆኑ አንጄል ዲማርያ በ65 ሚሊዮን ዩሮ፤ ፈረንሳዊው ፖል ፖግባና ጀርመናዊው ቶማስ ሙለር በ55 ሚሊዮን ዩሮ ከፍተኛ ዋጋቸው ይጠቀሳሉ፡፡ እስከ 10ኛ ደረጃ የሚሰጣቸውን ከፍተኛ የዝውውር ዋጋዎችም በትራንስፈርማርከት ድረገፅ ተመዝግበዋል፡፡ ማርዮ ጎትዜ፤ ኮኬ፤ ዲያጎ ኮስታ፤ ሮበርት ሌዋንዶውስኪ፤ ማርኮ ሬውስ፤ ቶኒ ክሮስ፤ ሉካ ሞድሪች ሰርጂዮ አጉዌሮ ካሪም ቤንዜማ እና ሴስክ ፋብሪጋስ በ50 ሚሊዮን ዩሮ ዋጋቸው ሲጠቀሱ፤ እነ አሌክሲ ሳንቼዝ፤ ሰርጂዮ ቡስኬትስ፤ ፋልካኦ በ45 ሚሊዮን ዶላር የዋጋ ከተማን የገበያውን ውድ ዋጋ ያገኛሉ፡፡
በትራንስፈርማርከት ድረገፅ ከላይ የተዘረዘሩት ተጨዋቾች በከፍተኛ የዝውውር ዋጋቸው ቢጠቀሱም ሲአይኢኤስ የተባለ የዓለም እግር ኳስ መረጃ አሰላሳይ ተቋም ባወጣው ጥናት በሚሰጣቸው የዋጋ ግምት የዘረዘራቸው ተጨዋቾች፤ ዋጋቸው እና ደረጃቸው ከዚህ የሚከተለው ነው፡፡ የተጨዋቾቹን ዋጋ ለማስላት ተቋሙ ከ2009 እኤአ ጀምሮ የተፈፀሙ ግብይቶችን አገናዝቧል።
ሊዮኔል ሜሲ 220 ሚሊዮን ዩሮ
ክርስትያኖ ሮናልዶ 133 ሚሊዮን ዩሮ
ኤዲን ሃዛርድ ቼልሲ 99 ሚሊዮን ዩሮ
ዲያጎ ኮስታ ቼልሲ 84 ሚሊዮን ዩሮ
ፖል ፖግባ ጁቬንትስ 72 ሚሊዮን ዩሮ
ሰርጂዮ አጉዌሮ ማን ሲቲ 65 ሚሊዮን ዩሮ
ራሂም ስተርሊንግ ሊቨርፑል 63 ሚሊዮን ዩሮ
ሴስክ ፋብሪጋዝ ቼልሲ 62 ሚሊዮን ዩሮ
አዘሌክሲ ሳንቼዝ አርሰናል 61 ሚሊዮን ዩሮ
ጋሬዝ ባሌ ሪያል ማድሪድ 60 ሚሊዮን ዩሮ
በዝውውር ከፍተኛ ገቢ ያገኙ ተጨዋቾች
ዝላታን ኢብራሞቪች በ7 ዝውውሮች 169.1 ሚሊዮን ዩሮ
ጄምስ ሮድሪጌዝ በ4 ዝውውሮች 132.63
ኒኮላስ አኔልካ በ8 ዝውውሮች 127.36
ሄርናን ክሬስፖ በ4 ዝውውሮች 119.27
ሴባስትያን ቬሮን በ6 ዝውውሮች 116
አንጄል ዲማርያ በ3 ዝውውሮች 116
ሊውስ ስዋሬዝ በ4 ዝውውሮች 115.8
ፋልካኦ በ4 ዝውውሮች 113.03
ሮናልዶ በሁለት ዝውውሮች 111.5
ጋሬዝ ባሌ በ2 ዝውውሮች 108.7
በዝውውራቸው ከፍተኛ ትፍ ያገኙ ተጨዋቾች
ጋሬዝ ባሌ 79.3 ሚሊዮን ዩሮ
ሮናልዶ 76.5
ዚነዲን ዚዳን 70 ሚሊዮን ዩሮ
ሊውስ ፊጎ 57.5
ሪካርዶ ካካ 56.75
ሊውስ ስዋሬዝ 54.5
ኤድሰን ካቫኒ 52.5
ሄርናን ክሬስፖ 51
ኢብራሞቪች 44.7
አንጄል ዲማርያ 42

      ለ31ኛው የአፍሪካ ዋንጫና ለ4ኛው የቻን ውድድር ለማለፍ በሚደረጉ ማጣርያዎች አመርቂ ውጤት ያስመዘገበው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን 2ኛ ምእራፍ ዝግጅቱን ከሁለት ሳምንት በኋላ እንደሚቀጥል ታውቋል። በሁለቱ አህጉራዊ ውድድሮች ዋልያዎቹ  ሦስት ጨዋታዎች በማድረግ በሁለቱ አሸንፈው በአንዱ አቻ ወጥተዋል፡፡ በ2017 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ በምድብ 10 ከአልጄርያ፤ ሌሶቶ እና ሲሸልስ ጋር የሚገኙት ዋልያዎች በምድብ ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታቸው ሌሶቶን በሜዳቸው 2ለ1 በማሸነፍ   በ3 ነጥብ በግብ ክፍያ በአልጄርያ  ተበልጠው መሪነቱን ተጋርተዋል፡፡ በቻን ቅድመ ማጣርያ ደግሞ ባለፈው ሰሞን ናይሮቢ ላይ ከኬንያ አቻቸው ጋር 0ለ0 ከተለያዩ በኋላ በ2ለ1 የደርሶ መልስ ውጤት ጥለው በማለፍ ለመጨረሻው ማጣርያ አልፈዋል፡፡ በአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ ቀጣይ ተጋጣሚያቸው ከሜዳ ውጭ ሲሸልስ ስትሆን በቻን የመጨረሻ ማጣርያ ደግሞ በደርሶ መልስ ከብሩንዲ ጋር ይገናኛሉ፡፡
ዋልያዎቹ ከሁለት ሳምንት ዕረፍት በኋላ ወደ ዝግጅታቸው ሁለተኛ ምእራፍ እንደሚገቡና  ለቀጣዩ ግጥሚያዎቻቸው መስራት እንደሚጀምሩ እና  በነሐሴ ወር ሁለት የወዳጅነት ጨዋታ በማድረግ አቋማቸውን እንደሚፈትሹ ይጠበቃል፡፡ ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በሜዳው ላይ እና ከሜዳው ውጭ የወዳጅነት ጨዋታዎች ለማድረግ የሚፈልጉ አገራት መበርከታቸውን ከፈዴሬሽኑ የሚወጡ መረጃዎች ይገልፃሉ፡፡
በ2017 የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ ከኢትዮጵያ ጋር ከተደለደሉት ቡድኖች በቻን ማጣርያቸው ሲሸልስ ስትወድቅ፤ ሌሶቶ ግን አልፋለች፡፡ ሲሸልስ በሞዛምቢክ 9ለ1 በሆነ የደርሶ መልስ ውጤት ተሸንፋ ስትወድቅ ፤ ሌሶቶ ደግሞ ቦትስዋናን ጥሎ በማለፍ ለመጨረሻ ዙር ማጣርያ በቅታለች፡፡ በመጨረሻ ዙር የቻን ማጣርያ የኢትዮጵያ ተጋጣሚ የሆነችው ብሩንዲ በቻን ውድድር ለመጀመርያ ጊዜ በ2014 ተሳትፋ የነበረ ሲሆን ሱዳንን በመለያ ምቶች 4ለ3 ጥላ በበማፍ ነበር፡፡ በ2009 እኤአ በደርሶ መልስ ማጣርያ ብሩንዲን ያሸነፈችው ሩዋንዳ ስትሆን በ2011 እኤ ደግሞ ኡጋንዳ ነበረች፡፡ ሲሸልስ በ2017 አፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ 2ኛ ጨዋታ ላይ ከኢትዮጵያ ጋር በሜዳዋ ከመገናኘቷ  በፊት ጠንካራ ዝግጅት ለማድረግ ወስናለች፡፡ አሰልጣኙ ማቲዮት ሰሞኑን በሰጡት መግለጫ ቡድናቸው ዛሬ እና ነገ ወደ አልጄርያ በማቅናት  የሁለት ሳምንት ዝግጅት በካፕ ተቀምጦ ያደርጋል፡፡ ከዚህ ዝግጅት በኋላም በኢንድያን ኦሽን ጌምስ በመካፈል ከማዳጋስካር ፤ ከማልዴቪስና  ከማዮቴ ደሴት ብሄራዊ  ቡድኖች ጋር በምድብ ማጣርያ ይጫወታል፡፡

Page 10 of 17