የማሪታይም ጉዳይ ባለሥልጣን የቀድሞውን ዕቅድ መነሻ በማድረግ፣ አፈጻጸሙን ጐዶሎ ያደረጉትን ትላልቅ ጉዳዮች ለይቶ በማውጣት የሚቀጥለው 5 ዓመት እቅድ የተሻለ እንዲሆን ከደንበኞችና ባለድርሻ አካላት ጋር ከትናንት በስቲያ በኢሊሌ ሆቴል ባደረገው ምክክር፤ በዕቅዱ 5 ዓመት መጨረሻ ከአፍሪካ ቀዳሚ ለመሆን እየሠራ መሆኑን አስታወቀ፡፡
የዓለም ባንክ ባለፈው 2014 ባወጣው ሪፖርት፤ የኢትዮጵያ የገቢና ወጪ ዕቃዎች የትራንዚት ጊዜ 44 ቀናት ይፈጃል ቢልም ባለሥልጣኑ የመረጃ ምንጭ ስህተት ነው በማለት አስተባብሏል፡፡
ባንኩ የኢትዮጵያ የገቢና ወጪ ዕቃዎች የትራንዚት ጊዜ በአማካይ 44 ቀናት ነው የሚለውን መረጃ ያገኘው ከእኛ ሳይሆን ስለ ኢትዮጵያ ወቅታዊ አፈጻጸም ትክክለኛ መረጃ ከሌላቸው ዓለም አቀፍ አስተላላፊዎች (Forwarders) ነው ያሉት የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ መኮንን አበራ፣ “ከባንኩ ጋር ፊት ለፊት ተገናኝተን ብንወያይ እንግባባ ነበር፡፡ እኛ ገቢና ወጪ ዕቃዎች ለማስተላለፍ የሚወስድብን ጊዜ በአማካይ ከ15-20 ቀን ሲሆን ይህም በዛ ብለን በቀጣዩ ዕቅድ መጨረሻ 50 በመቶ ለመቀነስ እየጣርን ነው” ብለዋል፡፡
44 ቀን ይፈጃል ማለት ለአንድ ኤክስፖርተር የሚሰጠው ትርጉም የተለየ ነው ያሉት ዳይሬክተሩ፣ ገንዘብ ኖሮት (ለጭነት፣ ለማጓጓዣ፣ ለጉምሩክ፣ ለወደብ፣ ለባንክ…) ከፍሎ አስፈላጊ ሰነዶችን ያሟላ ሰው ከ15 ቀን በላይ አይወስድበትም፡፡ ይኼ የመረጃ ክፍተት የውጭ ኢንቬስተሮችን በጣም ያስደነግጣል፡፡ አሁን ካለን አፈጻጸም አኳያ አንዳንድ ነጥቦች ከባንኩ ጋር አያስማሙንም፡፡ ምክንያቱም እኛ የምንለው በሐሳብ ላይ ተመስርተን ሳይሆን በተጨባጭ በተግባር እየተሰራ ያለውን ነው በማለት አስረድተዋል፡፡
ይህን የምንለው ሪፖርቱን ለመቃወም አይደለም፤ የኢትዮጵያ ሎጀስቲክስ ችግር አለበት በሚለው ነጥብ ላይ ከእነሱ በላይ እኛ እናምናለን፡፡
ምክንያቱም ልማታችን ከሚጠይቀው ፍጥነት አኳያ፣ ባጠረ ጊዜ፣ በተመጣጣኝ ዋጋ ኢምፖርት/ኤክስፖርታችን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ካልሆን ውጤት አናመጣም፡፡ ቁጥሩን ትተን “የኢትዮጵያ ሎጀስቲክስ ችግር አለበት” የሚለው በጣም ይስማማናል በማለት ገልጸዋል፡፡
በዓለም አቀፍ የሎጂስቲክስ አፈጻጸም መለኪያ መሰረት የኢትዮጵያ የዚህ ዓመት አፈጻጸም በአማካይ 2.59 ነጥብ፣ ከዓለም የአገሮች ደረጃ 104ኛ መሆኗን ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡  አቶ መኮንን በዓለም ባንክ መለኪያ መስፈርት መሰረት መካከለኛ ገቢ ላይ የደረሱ አገሮች ደቡብ አፍሪካ፣ ማላዊ፣ ዙንባብዌ፣ ሩዋንዳ፣ ታይላንድ፣ ቦሊቪያ፣ … በማሪታይምና በሎጅስቲክ የደረሱበትን ደረጃ በመገምገም ከ5 ዓመቱ ዕቅድ የአፈፃፀም አገራዊ፣ አኅጉራዊና ዓለም አቀፋዊ መልካም አጋጣሚዎችና ስጋቶችን በጥልቀት ፈትሸውና አገናዝበው በ2012 መጨረሻ ከቪየትናም፣ ኢንዶኔዥያ፣ ህንድና ፊሊፒንስ ተርታ ለማሰለፍ አሁን በአማካይ 2.59 የሆነውን አፈጻጸም በአማካይ 3.07 ለማድረስ፣ ደረጃውን ደግሞ ከ104ኛ ወደ 57ኛ ከፍ በማድረግ ከአፍሪካ 1ኛ ለማድረግ መወሰናቸውን ተናግረዋል፡፡
ዕቃዎች ወደብ ላይ የሚቆዩበትን ጊዜ ከ40 ቀን በላይ ወደ 3 ቀን ለመቀነስ፣ በኮንቴነር ታሽገው ሊጓጓዝ የሚችሉ ዕቃዎችን ከ7 በመቶ 100 ፐርሰንት ለማድረስ፣ የገቢ ዕቃ ፎርማሊቲዎችን ከ10 ወደ 4 ለመቀነስ፣ አሁን በእጅ የሚሰራውን ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂን በመጠቀም  100 ፐርሰንት አውቶማቲክ ማድረግ፣ ብቁ ባህረኞችን ለአገር ውስጥና ለውጭ አገር መርካቦች በማሰልጠን አሁን ያለውን 6000 ወደ 30,000፣ በውጭ አገር መርከቦች ላይ ተቀጥረው የሚሰሩ ኢትዮጵያውያን መርከበኞች ከሚያገኙት ገቢ 80 በመቶ ለቤተሰቦቻቸው ከሚልኩት 72 ሚሊዮን ዶላር ሬሚታንስ ወደ 0.3 ቢሊዮን ዶላር ማሳደግ፣ … የማሪታይም ጉዳይ ባለሥልጣን የ5 ዓመት ዕቅድ ነው፡፡
ኢትዮጵያ በአፍሪካ የራሳቸው የንግድ መርከቦች ካላቸው አገሮች አንዷ በመሆንዋ ቀደም ሲል በህንድና በጋና ይሰለጥኑ የነበሩትን መርከበኞችን ራሷ ከማሰልጠኗም በላይ በዓለም ላይ 450 ሺህ የባህረኞች እጥረት ስላለ ቀሪዎቹን በውጭ ምንዛሪ በአውሮፓ መርከቦች ላይ በመቀጠር ወደ አገር በሚልኩት ገንዘብ (ሬሚንታስ) ለአገራቸው የውጭ ምንዛሬ እንደሚያስገኙ ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ጊዜ በመካከለኛ ምስራቅ አገሮች የሚሰሩትን ሳይጨምር ከባህርዳር ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በኤሌክትሪካልና በሜካኒካል ኢንጂነሪንግ በዲግሪ የተመረቁ ከአንድ ሺህ በላይ መርከበኞች በትላልቅ መርከቦች ላይ በኦፊሰርነት ተቀጥረው እየሰሩ መሆኑን ገልፀዋል፡፡  ከፍተኛ ሥራ መሠራት አለበት ያሉት ዳይሬክተሩ፤ በአምስት ዓመቱ እቅድ መጨረሻ ከ10ሺህ እስከ 30ሺህ መርከበኞች ይሰለጥናሉ ብለዋል፡፡
አቶ መኮንን፣ ባለሥልጣኑ ያዘጋጀው እቅድ ሙሉ በሙሉ የሚሳካው፣ በባልሥልጣኑ ብቻ ሳይሆን እያንዳንዱ ባለድርሻ አካል (ጉምሩክ፣ ባንክ፣ ወደብ፣ ማጓጓዣ፣ ማሪታይም፣ ኢምፖርተርና ኤክስፖርተር…) ሁሉም ድርሻቸውን አውቀው በኃላፊነትና በተጠያቂነት በጋራ ሲሰሩ መሆኑን ጠቅሰው እቅዱን ስኬታማ ለማድረግ እንዲረባረቡ ጠይቀዋል፡፡   

ቤተሰቧና የአካባቢው ህብረተሰብ ለአምስት ቀናት ጭንቅ ውስጥ ነው የከረሙት፡፡ ባህላዊ መድሃኒቶችን ሲያደርጉና በየእምነታቸው ሲፀልዩ ሰንብተዋል፡፡ ደፍሮ ወደ ህክምና ተቋም የመውሰድ ሃሳብን የሰነዘረ ግን አንድም አልነበረም፡፡ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በሴት ልጆች ላይ የሚፈፀም ግርዛት ወንጀል እንደሆነ ሲነገር ሰምተዋል። ለዓመታት ከዘር ዘር ሲወራረስ የመጣውንና ሁሉም ሲፈጽመው የኖረውን ይህን የግርዛት ተግባር ወንጀል ነው ብሎ አምኖ መቀበል ለአካባቢው ህብረተሰብ እጅግ ከባድ ነበር፡፡ እናም ድርጊቱን በድብቅ ይፈጽሙታል፡፡ እንዲህ እንደአሁኑ ዓይነት ፈታኝ ገጠመኞች ካልደረሱ በስተቀር ማንም ይህንን ድርጊታቸውን ለማወቅና ለማስቆም ይችላል ብለው አያስቡም፡፡
የግርዛት አገልግሎቱን የሚሰጡት የ68 አመቷ ወ/ሮ፤ በአካባቢው ህብረተሰብ ዘንድ እጅግ የተከበረ ስምና ዝና ያላቸው፤ “እጅሽ ይባረክ” የተባለላቸው ባለሙያ ናቸው። በግርዛት ሥራ ላይ ከተሰማሩበት ካለፉት 40 ዓመታት ጀምሮ እስከዛሬም ድረስ ለበርካታ ወንድና ሴት ልጆች የግርዛት አገልግሎት ሲሰጡ ቆይተዋል፡፡ ቀደም ሲል ሥራቸውን የሚሰሩት በግልጽና በአደባባይ ነበር፡፡
በእጃቸው ተገርዘው አድገው የተዳሩ ሴቶች በርካታ ናቸው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ግርዛትን በአደባባይ መፈፀም አዳገታቸው፡፡ በሚስጢር ለማከናወንም ተገደዱ፡፡ የሴት ልጆች ግርዛት ለጤና ችግር የሚያስከትል እንደሆነና በወንጀል እንደሚያስቀጣም በወረዳው የሥራ ኃላፊዎች በተደጋጋሚ ተነግሮአቸዋል፡፡ ከድርጊታቸው እንዲታቀቡም አስጠንቅቀዋቸው ነበር፡፡
 “እናቴ ተገርዛለች፣ እኔንም አስገርዛኛለች እኔ ደግሞ ልጆቼን ገርዣለሁ፡፡ ግን ምንም አልሆንንም፡፡ መቼም የዛሬ ልጆች ሰለጠንን ብላችሁ የማታመጡት ነገር የለም” ሲሉ ይሟገታሉ ፤ የሴትን ልጅ ግርዛት ጉዳት አንስቶ ለሚሞግታቸው፡፡
ወይዘሮዋ የግርዛት አገልግሎት የሚሰጡበት ዕቃና ሥፍራ ንፅህናውን ያልጠበቀና ለበሽታ የሚያጋልጥ ነው፡፡ የሶስት ዓመቷ ህፃን የደረሰባትና ቤተሰቦቿንና የአካባቢዋን ሰዎች ጭንቅ ውስጥ የከተታቸውም በዚሁ ንፅህና በጐደለው ዕቃ በተደረገላት ግርዛት ሳቢያ የደረሰባት የጤና ጉዳት ነው፡፡ በግርዛት ሳቢያ ያለአግባብ ከተተለተለው የህፃኗ እምቡጥ ሰውነት ሌላ ኢንፌክሽኑ የፈጠረው የጤና ችግር ስቃይዋን እጥፍ ድርብ አድርጐባታል፡፡ ሁኔታዋ እየባሰ ሲሄድ ቤተሰቦቿ በአካባቢያቸው ወደሚገኝ የጤና ጣቢያ ይዘዋት ሄዱ፡፡ እንደ እሣት የሚፋጀው ሰውነቷ የሥቃይዋን መጠን አፍ አውጥቶ ይናገራል፡፡
በጤና ጣቢያው ምርመራ ያደረገላት ሃኪም ህፃኗ ንፅህናው ባልተጠበቀ መሣሪያ በተደረገላት ግርዛት ምክንያት ለከፍተኛ ኢንፌክሽን መጋለጧንና ይህም በወቅቱ ህክምና ባለማግኘቱ ወደከፋ ደረጃ መሸጋገሩን አረጋገጠ፡፡ ህፃኗ ለከፍተኛ ህክምና ወደ አዲስ አበባ መሄድ እንደሚኖርባትም ወሰነ፡፡ ሁኔታው እጅግ አሳዛኝ ነበር፡፡ ወላጆች የሶስት ዓመቷን ህፃን ይዘው ወደ አዲስ አበባ ቢመጡም ከሞት ሊታደጓት ግን አልቻሉም። በግርዛት ሳቢያ በተፈጠረባት ከባድ ኢንፌክሽን ህፃኗ ህይወቷን አጣች፡፡
ይህንን በአካባቢው ህብረተሰብ ዘንድ ከፍተኛ ሐዘን ጥሎ ያለፈውንና ከጥቂት ዓመታት በፊት በሥፍራው የተፈፀመውን ታሪክ ያጫወቱኝ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል በጋሞጐፋ ዞን ቁጫ ወረዳ በምትገኝ አንዲት የገጠር ቀበሌ ውስጥ ያነጋገርኳቸው የ72 ዓመቱ የዕድሜ ባለፀጋ አቶ ዋቴሮ ዳልኬ ናቸው። ሥፍራው የሴት ልጅ ግርዛት፣ ያለዕድሜ ጋብቻ፣ ጠለፋና፣ የጉልበት ብዝበዛ በስፋት የሚከወንበት ሥፍራም እንደሆነ ይነገራል፡፡ ችግሩ በተለይ ቀደም ባሉት ዓመታት በስፋት የሚታይ እንደነበርና ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ እየቀነሰ መምጣቱን ነግረውኛል፡፡ የአካባቢው ማህበረሰብ ሴት ልጆችን ወደ ትምህርት ቤት መላክ አግባብ እንዳልሆነ የሚያምን ሲሆን ሴቶች ልጆች በቤት ውስጥ ሥራ እናታቸውን ከማገዝና በላይ በላይ የሚወለዱ እህት ወንድሞቻቸውን ከማሳደግ የዘለለ ተግባር እንደማያከናውኑም አቶ ዋቴሮ ዳልኬ ነግረውኛል፡፡
ያለዕድሜ ጋብቻን አሊያም ጠለፋን በሚፈጽሙ ወንጀለኞች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ጠንካራ  ባለመሆኑ ድርጊቱ አሁንም ድረስ መቀጠሉን አዛውንቱ አጫውተውኛል፡፡ ከዓመታት በፊት በ3 ዓመቷ ህፃን ላይ የደረሰውንና ለሞት ያበቃትን ጉዳይ ግርዛቱ ምርቅዝ ሆኖባት ሲሉ ይገልፁታል እንጂ በመገረዟ ምክንያት ለችግር መጋለጧን አያምኑም፡፡ እሣቸውም የወለዷቸውን አራት ሴት ልጆች በእኚሁ ሴት ማስገረዛቸውን አልሸሸጉም፡፡ “ሴት ልጅ ካልተገረዘች አታድብም፣ እግር ታወጣለች፣ እቃ አይበረክትላትም” ሲሉ ይናገራሉ - አዛውንቱ፡፡    
“የጋራ ጥረታችንን በማጐልበት ያለ ዕድሜ ጋብቻን እናስቁም” በሚል መሪ ቃል የተከበረውን የዘንድሮውን የአፍሪካ ህፃናት ቀን በዓልን፣ ፕላን ኢንተርናሽናል ከወላይታ ልማት ማህበር ጋር በመተባበር በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል በወላይታ ዞን ሶዶ ከተማ ውስጥ አክብሯል፡፡ በዚህ በዓል ላይ በክልሉ የሚፈፀሙና ሴቶችን ለከፍተኛ ችግር የሚያጋልጡ ጐጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን አስመልክቶ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ውይይት ተደርጐባቸዋል፡፡ በወላይታ ዞን ሴቶች ህፃናትና ወጣቶች ጉዳይ መምሪያ የቀረበ አንድ ጥናት እንደሚያመለክተው፤ ክልሉ የሴት ልጅ ግርዛት፣ በህፃናት ላይ የወሲብ ጥቃትን መፈፀም፣ ለወንድ ህፃናት ቅድሚያ መስጠት፣ ጠለፋ፣ ድርብ ጋብቻ፣ ያለዕድሜ ጋብቻና የህፃናት ጉልበት ብዝበዛ ---- በሥፋት የሚፈጸምበት ሥፍራ ነው፡፡
የሴት ልጅ ግርዛትን አስመልክቶ ጥናቱ ይፋ ባደረገው መረጃ፤ በክልሉ ወላይታ ዞን በሁሉም ወረዳዎች በገጠርና ከተማ፣ በሁሉም የክርስትና እና የእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ ግርዛት ይፈፀማል። ባለፈው አመት የዞኑ ሴቶች ህፃናትና ወጣቶች ጉዳይ መምሪያ ባደረገው ጥናት፣ ዕድሜያቸው ከ7-10 ከሆነ 1094 ሴቶች መካከል 600 የሚሆኑት (ከግማሽ በላይ) ሴቶች ተገርዘዋል፡፡ የአካባቢው ማህበረሰብ በሴት ልጆች ላይ ግርዛት ከሚፈጽምባቸው ምክንያቶች መካከል፡- ሴት ልጅን ቀዝቃዛና የተረጋጋች ለማድረግ፣ የወሲብ ፍላጐቷን ለመቀነስና፣ ድንግልናዋን ለመጠበቅ የሚሉት የሚጠቀሱ ሲሆን ግርዛቱ በባህላዊ መንገድና በድብቅ እንደሚፈጸምም ጥናቱ ጠቁሟል። ሴቶች በግርዛት ሳቢያ የሚደርስባቸው የጤና ችግሮች በሚል ጥናቱ ከጠቀሳቸው መካከል፤ ውስጥ ደም መፍሰስ፣ ቴታኖስ (ኢንፌክሽን) ሽንት የመሽናት ችግርና ሞት ይገኙባቸዋል፡፡
የህፃናት ጉልበት ብዝበዛን አስመልክቶ በጥናቱ ላይ የሰፈረው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ ህፃናት ከትውልድ ቀዬአቸው ተፈናቅለው ወደ ከተማ ሲወጡ የተሻለ ኑሮ ይኖራሉ፤ ቤተሰቦቻቸውንም ይደጉማሉ በሚል መነሻ ከዞኑ ውጪ በሚገኙ ከተሞች፣ በኦሮሚያ ክልል ገጠር አካባቢዎች እንዲሰደዱ ይደረጋሉ፡፡  ከ2004-2005 ዓ.ም ባለው የአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ብቻ 1442 ህፃናት ከተለያዩ ገጠር ወረዳዎችና ከተሞች የህገወጥ አዘዋዋሪዎች ሰለባ በመሆን ሄደው፣ በአስቸጋሪ ሁኔታ ከሚገኙበት ሥፍራ ተይዘው ወደየወላጆቻቸው እንዲመለሱ ተደርገዋል፡፡  
ያለዕድሜ ጋብቻን አስመልክቶም በጥናቱ ላይ የሰፈረው መረጃ እንደሚያመለክተው ሴት ልጅን ያለ ፍላጐቷ በማስገደድ የሚፈፀሙ ጋብቻዎችና ጠለፋ በስፋት ይታያሉ፡፡ በተለይም በዞኑ ቆላማና ዳር በሆኑ ወረዳዎች ማለትም በሁምቦ፣ በዳወይዴ፣ ቦሎሶ ቦንቤ፣ ኪንዶ ኦይሻ፣ ኪንዶ ዲዳዬ፣ ዳሞት ፑላስ፣ ዳሞት ሶሬና ዱጉና ፉንጐ ወረዳዎች ላይ ድርጊቱ በስፋት ይፈፀማሉ፡፡
ፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ በተለያዩ ጐጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ማለትም ያለዕድሜ ጋብቻ፣ በጠለፋ፣ በአስገድዶ መድፈር፣ በጉልበት ብዝበዛና በሌሎችም ምክንያቶች ትምህርት ያጡ ህፃናት ችግሮቻቸውን በመቅረፍ ትምህርታቸውን ለመከታተል የሚችሉበትን መንገድ በማመቻቸቱ ረገድ በክልሉና በዞኑ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል፡፡ ከእነዚህ ተግባራት መካከልም በዞኑ ገጠራማ አካባቢዎች በሚገኙ አንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች ውስጥ የተሰሩትና በድርጅቱ ድጋፍ የሚደረግላቸው ማዕከላት ይጠቀሳሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ድርጅቱ ከሳምሰንግ የኤሌክትሮኒክስ ኩባንያ ጋር በመተባበር በፀሐይ ኃይል የሚሰራ ተንቀሳቃሽ የኮምፒዩተር ማስተማሪያ ክፍል በክልሉ ጋሞጐፋ ዞን ቁጫ ወረዳ ዲንኬ ሙሉ አንደኛ ደረጃ ት/ቤት ውሰጥ አቋቁሟል፡፡
በአንድ ጊዜ 25 ተጠቃሚዎችን የማያስተናግደው ይኸው የኮምፒዩተር ማስተማሪያ ማዕከል በ65 ኢንች ዲጂታል ስክሪን ተማሪዎችን የኮምፒውተር ዕውቀት ለማስጨበጥ እንዲያስችል ተደርጐ የተሰራ ነው፡፡ በማዕከሉ ውስጥ የሚገኙት ሃያ አምስት ዘመናዊ ላፕቶፕ ኮምፒውተሮች የኢንተርኔት አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ ለማድረግ ጥረት በመደረግ ላይ እንደሆነም በማዕከሉ የምረቃ ፕሮግራም ላይ ተገልጿል፡፡
የጋሞጐፋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የፋይናንስና ኢኮኖሚ መምሪያ ኃላፊ አቶ ተፈሪ አባተ በማዕከሉ ምረቃ ላይ እንደተናገሩት ድርጅቶቹ ህፃናትን በማስተማርና በማብቃት ተግባሩ ላይ እያከናወኑ ያሉትን ተግባር አድንቀው ህፃናት የነገ አገር ተረካቢ ችግኞች በመሆናቸው በችግኙ ላይ መሥራት የተሻለ ምርትን ለማግኘት ያስችላል ብለዋል፡፡
በዞኑ ቀደም ሲል በስፋት ይታዩ የነበሩት ጐጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ቀንሰው ሴቶች ከወንዶች እኩል በትምህርቱም ሆነ በልማቱ ዘርፍ ተሳታፊ የሚሆኑበት ዘመን እንዲመጣም ምኞታቸውን ገልፀዋል፡፡
በሴቶች ላይ የሚፈፀሙ ግርዛትን ጨምሮ ሌሎች ጐጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን በማስወገድ ሴት ልጆችን ለማብቃት የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል። ፕላን ኢንተርናሽናል እነዚህን ጐጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ለማስወገድና በሴቶች ላይ የሚፈፀሙ ወንጀሎችን ለማስቆም የሚያደርገው ዘመቻም ሊበረታታ የሚገባው ነው፡፡ ሴት ልጅን ማስተማር ህብረተሰብን ማስተማር እንዲሉ ነውና፡፡

Published in ዋናው ጤና

ሰሞኑን በሂልተን ሆቴል በተካሄደ ወርክሾፕ ላይ የቀረበ ጥናታዊ ጽሑፍ፣ እኛ እንደማባያ (ወጥ) የምንጠቀማቸው ጥራጥሬዎች በአሁኑ ወቅት በመላው ዓለም ተፈላጊነታቸውና ዋጋቸው መጨመሩን አመለከተ። ኢትዮጵያ ለእነዚህ ምርቶች ተስማሚ አየር ንብረትና አመቺ ሁኔታ ስላላት፣ በብዛትና በጥራት እያመረተች ለዓለም ገበያ ብታቀርብ፣አሁን ከምታገኘው ከሁለትና ሦስት እጥፍ በላይ ገቢ እንደምታገኝ በጥናቱ ተጠቁሟል፡፡  
ወርክሾፑን ያዘጋጀው በተባበሩት መንግሥታት ዓለም አቀፍ የንግድ ማዕከል Supporting Indian Trade and Investment for Africa (SITA) ከ2014 – 2020 የህንድና የአምስት የምስራቅ አፍሪካ አገሮች ኢንቬስትመንት፣ ኤክስፖርት ስትራቴጂና የተወዳዳሪነት አቅም በማጎልበት ለመደገፍ የተቋቋመ ፕሮጀክት ተቋም ነው፡፡
በእንግሊዝ ህዝብና በሰሜን አየርላንድ መንግስት የገንዘብ ድጋፍ የሚንቀሳቀሰው ሲታ ፕሮጀክት ዓላማ፤ እንደ ህንድ ዓይነት በመበልፀግ ላይ ያሉ አገራት ዓለም አቀፍ የዕድገት ሰንሰለት  ወደ ምስራቅ አፍሪካ አገሮ እየተስፋፋ ስለሆነ በህንድ፣ ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ሩዋንዳ፣ ዩጋንዳና ታንዛኒያ----ንግድና በኢንቨስትመንት፣ የኢኮኖሚ ዕድገት፣ የሥራ ዕድል ፈጠራና ድህነት ቅነሳ የሚደረገውን እንቅስቃሴ መደገፍ ነው፡፡ ፕሮጀክቱ፣ በአሁኑ ወቅት ህንድ የደቡብ ደቡብ ነፃ የንግድ ግንኙነት ቀጣና በሰጠችው ነፃ የታሪፍ ተጠቃሚነት ዕድል፣ በማደግ ላይ ያሉ ከአምስቱ የምሥራቅ አፍሪካ አገሮች ወደ ህንድ የሚገቡ ምርቶች 98 በመቶ ከቀረጥ ነፃ የታሪፍ ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑ ተገልጿል፡፡
በወጪ በጥራጥሬ ንግድ ላይ ለተሰማሩ የኢትዮጵያ ድርጅቶች፣ ለመንግሥት ኃላፊዎችና ጉዳዩ ለሚመለከታቸው አካላት ለሁለት ቀን የተዘጋጀውን ወርክ ሾፕ የመሩት በተባበሩት መንግስታት የዓለም አቀፍ የንግድ ማዕከልና የዓለም የንግድ ድርጅት አባል እንዲሁም የንግድ ድጋፍ ማጠናከሪያ ተቋም ሲታ አማካሪ ሚ/ር አማን ጎል ኃላፊነታቸው፣ በማደግ ላይ ያሉ አገራት ንግድና ኢንቨስትመንት ለማቀላጠፍ በሦስት ደረጃ ላሉት ተሳታፊዎች ስልጠና እንደሰጡ ጠቅሰው፣ ፖሊሲ አውጪዎች፣ ለጥራጥሬ የንግድ ዘርፍ አመቺና ተስማሚ የሆነ ፖሊሲ እንዲቀርፁ፣ በአገር ውስጥና በውጭ ንግድ የተሰማሩ ድርጅቶች የአቅም ግንባታና በጥራጥሬ ንግድ ለመሰማራት ፍላጎቱ እያላቸው አሰራሩን ለማያውቁ ግለሰቦች ትምህርት መስጠታቸውን ተናግረዋል፡፡
ኢትዮጵያ ለጥራጥሬ ምርት አመቺ የሆነ እምቅ ሀብት፣ እውቀትና ልምድ ቢኖራትም ከአገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ በዘርፉ በውጭ ንግድ ተሰማርታ ማግኘት የሚገባትን ጥቅምና ገቢ አላገኘችም ያሉት ሚ/ር ጎል፣ ህንድና ሌሎች ገበያዎች የእነዚህ የእርሻ ውጤቶች ፈላጊ ናቸው፡፡ በውጭ ንግድ የተሰማሩ ድርጅቶች ዓለም አቀፍ ገበያው (በአሜሪካና በአውሮፓ) በሚፈለገው የጥራት ደረጃና መጠን ለማቅረብ የአቅም፣ የቴክኖሎጂ፣ የእውቀት ውሱንነት አለባቸው፡፡ የህንድ ፍላጎት፣ ለጥራጥሬ የወጪ ንግድ አስፈላጊ የሆኑ መሳሪያዎችና እውቀት ከአሜሪካና ከአውሮፓ አምጥቶ፣ ኢትዮጵያ እንድታመርትበትና በአገሪቷ በጥራጥሬ ምርት ዘርፍ ኢንቬስት ማድረግ ነው። በርካታ የህንድ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ኢንቨስት ማድረግ ይፈልጋሉ፡፡ በዚህ ወርክሾፕም ሁለት የህንድ ኢንቬስተሮች ተገኝተዋል፤ በማለት የሲታን አስፈላጊነት አብራርተዋል፡፡
ህንድ የምትፈልገው የምርት ብዛት ብቻ ሳይሆን ዓይነቱ በዝቶና እሴት ተጨምሮበት ኤክስፖርት እንዲደረግ ነው፡፡ በቀጣይ 5 ዓመት የተሻለ ነገር እንደምናይ ተስፋ አደርጋለሁ ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ በጥራጥሬ ምርት ለዘመናት የካበተ ልምድና እውቀት አላት፡፡ አሁንም‘ኮ እያመረተች ነው፡፡ ነገር ግን ከሚመረተው ውስጥ ከ70 እስከ 75 በመቶ ለአገር ውስጥ ፍጆታ እንደሚውል ተገንዝቤአለሁ፡፡ መንግስትም ምርቱ ለውጭ ገበያ ቢቀርብ ጠቃሚነቱ የጎላ መሆኑን አምኗል። አሁን የምናደርገው ዓለም አቀፍ የጥራት ደረጃ ያሟላ ምርት ለማግኘት፣ በእርሻ ወቅትና ከእርሻ በፊት በዝግጅት ወቅት መደረግ ስላለበት ጥንቃቄ፣ ከምርት በኋላ ምርቱ ለገበያ እስኪቀርብ ድረስ የሚፈጠረውን ብክነት፣ ዋጋ እንዲንር የሚያደርጉ አቀባባዮች የሚቀነሱበትን መንገድ መፈለግ፣ አምራቾችና  ነጋዴው ፊት ለፊት ተገናኝተው የሚገበያዩበትን ዘዴ መፍጠር ነው ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ ለውጭ ገበያ የምታቀርባቸው ምርቶች በዓለም በጣም ምርጥ ከተባሉ ዝርያዎች አንዱ ስለሆኑ የህንድ ነጋዴዎች የኢትዮጵያን ምርት ለመግዛት ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው አማካሪው ተናግረዋል፡፡ አንድ ቅሬታ ግን አላቸው፡፡ በህንድ ገበያ ሽንብራ፣ ምስር፣ የእርግብ አተር ማሾ ተፈላጊ የሆኑት ጥራጥሬ ምርቶች ሲሆኑ ህንዶች የሚፈልጉት የሽንብራ መጠን ትልልቅ ሲሆን የኢትዮጵያ ምርት ግን ትንንሽ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ከመንግስት አካላት ጋር ተናጋግረናል፡፡ መንግስት በጣም ተባባሪ ከመሆኑም በላይ በዚህ ወርክሾፕም እየተሳተፈ ስለሆነ ችግሩ የሚወገድበት መንገድ እንደሚቀየስ እምነቴ ነው በማለት ገልፀዋል፡፡
ሚ/ር አማን በጥራጥሬ ምርት የሚታዩ ችግሮችንም ጠቅሰዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ለዓለም ገበያ ከሚቀርቡ 12 ዓይነት ምርቶች ውስጥ ከፍተኛውን ደረጃ፣ ከሶስት እጅ ሁለቱን ወይም 2/3ኛ የያዙት ሶስት ምርቶች፡- ባቄላ፣ ሽንብራና አተር ናቸው፡፡ ለገበያ የሚቀርቡ ምርቶች በዓይነት እንዲበዙ ይፈለጋል፡፡ የምርት ጥራትና ብዛት ማነስ፣ የሰለጠነ የሰው ኃይል እጥረት፣ የትራንስፖርት፣ የፓኬጂንግ ጉድለት፣ የአመራረት ችግር፣ መንግስትና የግሉ ዘርፍ ተቀናጅቶ ያለመስራት፣ አዳዲስ ገበያዎችን ያለመፍጠርና ሌሎች በርካታ ችግሮች ተጠቅሰዋል፡፡
የኢትዮጵያ ወጪ ንግድ የተመሰረተው በእርሻ ውጤቶች ላይ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ቡና 28.02 በመቶ የውጭ ምንዛሬ በማስገኘት ቀዳሚ ነው፡፡ የቅባት እህሎች 14.69 በመቶ፣ ጥራጥሬ ደግሞ 6.33 በመቶ ድርሻ በመያዝ 2ኛ እና 3ኛ ደረጃ ይዘዋል፡፡
ቻይና፣ ሶማሊያ፣ ጀርመን፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ ኔዘርላንድና አሜሪካ ከፍተኛ የኢትዮጵያ ምርት ገዢ አገሮች ሲሆኑ ወደ ጀርመን፣ የተባበሩት አረብ ኢመሬትስ፣ ሱዳን፣ እስራኤልና ኢጣሊያ ለማስፋፋት ዕቅድ ተይዟል። በፈጣን እድገት ላይ ካሉ አገሮች የኢትዮጵያን ምርት የሚፈልጉት ሰርቢያ፣ ሊቢያ፣ ቪየትናም፣ ጆርጅያ፣ ኩዌትና ጊኒ ናቸው፡፡
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንትና አግሪ ቢዝነስ ዘርፍ ለጥራጥሬ ምርት አመቺ ስለሆነ በጥሩ የሎጅስቲክስና የማከፋፈያ አውታሮች ቢታገዝ አገሪቱ የምስራቅ አፍሪካ የጥራጥሬ ማዕከል መሆን ትችላለች ተብሏል፡፡ ለውጭ ገበያ የሚቀርበው ጥራጥሬ አስተማማኝና የማያቋርጥ መሆን እንዳለበት የተጠቀሰ ሲሆን ከጎረቤት ጥራጥሬ አምራች አገሮችም ጋር መወዳደር እንዳለባት ተነግሯል፡፡   

     የቀዝቃዛው ጦርነት ከማክተሙ፤ የበርሊን ግንብ ከመደርመሱ፤ ዓለም ከአንድ የኃይል ዙፋን ሥር ከመውደቋ፤ ሩሲያ ከመፈራረሷ፤ ዓለም ‹‹ለሁለት ጣኦት አልገዛም›› ብላ፤ ‹‹ሊበራልዝም›› ለተሰኘው አማልክት ከመስገዷ በፊት፤ …. ያኔ በፊት፤ ታሪክ የማያቋርጥ ሂደት ሆኖ ይታይ ነበር፡፡ ታሪክ መጨረሻ አልነበረውም፡፡
ሆኖም፤ የቀዝቃዛው ጦርነት ሲያከትም፤ የበርሊን ግንብ ሲፈርስ፤ ዓለም ‹‹ሶሻሊዝም እና ሊበራሊዝም ለተባሉ ሁለት ጣዖታት አልገዛም›› ብላ ስትፈጠም፤ ብቸኛ ልዕለ ኃያል ሐገር ሆና ከወጣችው ከአሜሪካ ዙፋን ሥር ስትነጠፍ፤ አንድ ፍራንሲስ ፉኩያማ የሚሉት ፀሐፊ፤ ‹‹ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ፤ ዓለም የጀመረችው አንድ የታሪክ ጉዞ ከመጨረሻው ምዕራፍ ደረሰ›› የሚል ድፍረትን ተሻግሮ፤ ‹‹ራሱ ታሪክ ከጉዞው የመጨረሻ ምዕራፍ ደረሰ›› ብሎ አወጀ፡፡ ‹‹The end of history›› አለ፡፡ በዘመነ ፉኩያማ፤ ታሪክ መጨረሻ አገኘ።
ፍራንሲስ ፉኩያማ፤ ‹‹አሁን የምንገኘው፤ ከምዕራቡ ዓለም የተወለደው የሊበራል ዲሞክራሲ አገዛዝ፤ የሰው ልጆች ሁሉ በዕድገት ሂደት የሚቀበሉት አማራጭ የለሽ እና አይቀሬ ርዕዮተ ዓለም ወይም የአገዛዝ ስርዓት መሆኑን በሚያስረዳ የታሪክ የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ ነው›› ሲል በታሪክ ላይ የሞት ፍርድ አሳልፎ ነበር፡፡
ፉኩያማ ‹‹ታሪክ ሞተ›› ባለ ጊዜ (በ1980ዎቹ)፤ በአፄ ቴዎድሮስ ዘመን ተፀንሳ፤ በአፄ ዮሐንስ ጎልምሳ፤ በአፄ ምኒልክ ዘመን የመጨረሻ መልኳን ይዛ የተወለደችው እና በአፄ ኃይለ ስላሴ ዘመን ጠንካራ ማዕከላዊ አስተዳደር መስርታ፣ በኋላም ኤርትራን አካታ የቆመችው ኢትዮጵያ፤ ለረጅም ዘመናት በብዙ ቅራኔዎች ተቀስፋ የቆየችው ኢትዮጵያ፤ በመጨረሻ ከአረመኔው ደርግ እጅ ወድቃ ለ17 ዓመታት የማቀቀችው ኢትዮጵያ፤ የበርሊን ግንብ በፈረሰ ‹‹ሰሞን››፤ የአዲስ ስርዓት ምጥ ይዟት ተፋፍማ ነበር፡፡
ምናልባት፤ ፉኩያማ ‹‹የታሪክ መጨረሻ ሆነ›› ማለቱን የሚቃወሙና የተቃወሙ ሰዎች ቢኖሩም እንኳን፤ በደርግ መንግስት ውድቀት ማግስት የነበረውን የኢትዮጵያን ሁኔታ ያየ ሰው፤ ‹‹አሁን የዘመናዊት ኢትዮጵያ የመጨረሻ ዘመን ደረሰ›› የሚል የታሪክ ፍርድ ለመቀበል የሚቸገር አይመስለኝም፡፡ ወይም ተቃዋሚዎቹ ብዙዎች አይሆኑም ብዬ እገምታለሁ፡፡
ዛሬ - ዛሬ፤ ‹‹ፉኩያማ ‹ታሪክ ሞተ› ሲል፤ ታሪክ በበኩሉ፤ ‹ፉኩያማ ሞተ› አለ›› እያሉ የፉኩያማን ሐሳብ የሚነቅፉ ሰዎች በርክተዋል፡፡ እርሱም ሐሳቡን እንደቀየረ ይነገራል፡፡ ሆኖም በዚህ መጣጥፍ ማንሳት የፈለግኩት፤ የዓለምን የርዕዮተ - ዓለም ታሪክ መተረክ አይደለም። ጨርሶ የፉኩያማን ሐሳብ የመደገፍ ወይም የመንቀፍ ፍላጎት የለኝም፡፡ የኔ ትኩረት፤ ከፀሐፊው ሳይሆን ከቀልብ ሳቢው መፅሐፍ ርዕስ ነው፡፡ የፉኩያማ መፅሐፍ ርዕስም፤ ‹‹The end of history and the last man›› (የታሪክ መጨረሻ እና የመጨረሻው ሰው) የሚል ነው። ታዲያ ፉኩያማ ለመፅሐፉ የሰጠው ይህ ርዕስ፤ የአንድ ኢትዮጵያዊ መሪን ታሪክ፤ በብዙ ጎዳና (በእማሬም ሆነ በፍካሬ) ለመግለፅ የሚያስችል ልዩ አንደበት ወይም ቋንቋ ያለው ሆኖ ታየኝ፡፡
‹‹የታሪክ መጨረሻ እና የመጨረሻው ሰው›› የሚለው ሐረግ፤ የዚህን መሪ እና የሐገሪቱን፤ ምናልባትም የወቅቱን የዓለም ሁኔታ አሟልቶ ለመግለፅ የሚችል ነው፡፡ የፍራንሲስ ፉኩያማ መፅሐፍ ርዕስ፤ የኢትዮጵያ የታሪክ ፀሐፊዎች፤ ‹‹ዘመነ መሳፍንት›› በሚል በሚጠቅሱት የታሪክ ዘመን መጨረሻ ለመጡት እና የ‹‹ዘመነ መሳፍንት›› የመጨረሻው ንጉስ ለሆኑት ለአፄ ቴዎድሮስ ዘመነ መንግስት እና ህይወት ተገቢ ርዕስ መሆኑ ይታየኛል፡፡
በትውልድ ጃፓናዊ፣ በዜግነት አሜሪካዊ የሆነው ፍራንሲስ ፉኩያማ፤ ‹‹በታሪክ ላይ ሞት ከመፍረዱ አስቀድሞ›› ከ121 ዓመታት በፊት፤ የኢትዮጵያ የታሪክ ፀሐፊዎች፤ ‹‹ዘመነ-መሣፍንት›› ሲሉ በሚጠቅሱት የታሪክ ምዕራፍ (ከ1769 እስከ 1855 ዓ.ም እኤአ) ብቅ ካሉት አፄ ቴዎድሮስ ጋር ተያይዞ፤ በዓለም የጋዜጠኝነት ታሪክ አንድ አዲስ ነገር ተከስቷል፡፡ ይህ መጣጥፍ ትኩረት የሚያደርገው በዚሁ ጉዳይ ነው፡፡
እስራኤላውያን ጠቅልሎ የሚገዛ ንጉሥ አጥተው፤ የተለያዩ ግዛቶች በተለያዩ መሣፍንት ይገዙ የነበረበትን ሁኔታ መሰረት አድርገው፤ የኢትዮጵያ የታሪክ ፀሐፊዎች ‹‹ዘመነ-መሣፍንት›› ሲሉ በሚጠቅሱት ታሪከ - ዘመን የመጡት እና አንዳንድ ፀሐፊዎች የዘመነ-መሳፍንት የመጨረሻው መሪ አድርገው የሚመለከቷቸው፤ ሌሎች ደግሞ የአዲስ ዘመን ከፋች እና የዘመናዊት ኢትዮጵያ መስራች አባት አድርገው የሚያይዋቸው አፄ ቴዎድሮስ፤ ‹‹በታሪክ መጨረሻ የመጡ፤ የመጨረሻ ሰው›› ናቸው፡፡  
አፄ ቴዎድሮስ፤ በመጨረሻዋ ሰዓት መቅደላ አምባ ነበሩ፡፡ መቅደላ አፋፉ ላይ ቆመው፤ ከእንግሊዝ የኢንዱስትሪ አብዮት ማህፀን ከተወለደው እና ሊቀስሙት ይመኙት ከነበረው የአውሮፓ ስልጣኔ ጋር ተጋጥመው፤ ጠላቶቻቸውን ‹‹አሸነፍነው›› ብሎ ለመፎከር የሚያስቸግር ሁኔታ ውስጥ ከትተው ተሸነፉ። ዝርዝሩን ትተን በዋናው ጉዳይ ካተኮርን፤ በመቅደላ አምባ ጦርነት የገጠሙት ስልጣኔ እና ኋላ ቀርነት ናቸው ማለት እንችላለን፡፡
ኢትዮጵያ ከስልጣኔ ማማ ወርዳ ከኋላ ቀሮች መንድር ስትገባ፤ እንግሊዝ ወይም ጠቅላላው የአውሮፓ ህዝብ፤ ያልሰለጠነ የ‹‹ከፊል አውሬ›› ደረጃ ሊባል ከሚችል አዘቅት ወጥተው ዕድገትን ተቀዳጁ፡፡ እንግሊዝ ‹‹ባርባር›› በነበረች ዘመን፤ ህንድ እና ቻይና - በእስያ አህጉር፤  ኢትዮጵያ እና ግብፅ ደግሞ በአፍሪካ አህጉር የላቀ የስልጣኔ ደረጃ ላይ ደርሰው ነበር፡፡ ሆኖም፤ ወደ ኋላ፤ የተቀረው ዓለም መራመድ ተስኖት ቆሞ ሲቀር እና በታሪክ ጫማ እንደ በረዶ ተንኮታኩቶ ሲቀበር ወይም ምስጥ እንደበላው ውዳቂ ግንድ በታሪክ ደንታ ቢስ እግር እየተረጋገጠ ሲሰባበር፤ በኢንዱስትሪ አብዮት ከመሬት ተነስታ ጥበብን የታጠቀችው እንግሊዝ፤ የጥንታዊ ስልጣኔ ባለቤት የነበረችውን ህንድን፤ ጥበብን መሰረት ባደረገ ወታደራዊ ኃይል አንበርክካ ቅኝ ግዛቷ አደረገቻት።
የቻይናም ዕጣ ከዚህ ብዙ የራቀ አልነበረም፡፡ ቻይና በቀጥታ በቅኝ ግዛት ሥር ባትወድቅም፤ በእጅ አዙር የኃያላን መጫወቻ ሆናለች፡፡ ቻይና፤ ልክ እንደ ኢትዮጵያ፤ በየአካባቢው የተነሱ የጦር አበጋዞች ‹‹ዘመነ መሳፍንት›› ሰርተውባት፤ እንደ ቅርጫ ተቀራምተዋት ፍፁም ደክማ፤ የኃያላኑ መጫወቻ ሆናለች፡፡ በቴዎድሮስ ዘመን፤ ሌላዋ የጥንታዊ ስልጣኔ ባለቤት ግብፅ፤ በኃያላኑ እጅ ከወደቀች ብዙ ቆይታለች፡፡ የቀረችው ኢትዮጵያ ነች፡፡ ኢትዮጵያም ዙሪያዋን በቅኝ ገዢዎች ተከባ ቀኗን የምትጠብቅ መስላለች፡፡
በዚህ ጊዜ፤ እንደ አፄ ቴዎድሮስ ሁሉ፤ በወቅቱ የሚታየው ነገር አላምር ብሏት ጭንቀት ወርሷት የነበረችው ጃፓን፤ አዝማሚያውን ካየች በኋላ፤ ህልውናዋን ለማረጋገጥ የምትችለው የምዕራቡን ዓለም ቴክኖሎጂ በመቅዳት እንደሆነ ተረድታ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ መሳፍንት በአንድ ንጉስ መተዳደርን እምቢ ብለው ጦርነት ያደርጉ ነበረ፡፡ በዚያ ጊዜ፤ የጃፓን መኳንንት  እና ህዝቡ በአንድ ንጉስ ሥር ጠንካራ አንድነት በመመስረት፤ በፍጥነት የአውሮፓን ስልጣኔ መቅሰም እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ስለተረዱ፤ መኳንንቱ ሁሉ አውሮፓን ዞሮ ለማየት ተንቀሳቀሱ፡፡
‹‹የጃፓን መሳፍንት ይህን ውሳኔ እንዴት ሊወስኑ ቻሉ?›› የሚለው ጥያቄ፤ እንቆቅልሽ ሆኖ፤ የማህበራዊ ሳይንስ ጠቢባንን እስከዛሬ ያከራክራል፡፡ ሆኖም፤ ጃፓናውያን ነባር የፖለቲካ እና ባህላዊ አወቃቀራቸውን እንዳለ ጠብቀው፤ የኢኮኖሚ ስርዓታቸውን በካፒታሊዝም ለመቃኘት መነሳታቸው የማያከራክር እርግጠኛ ታሪክ ነው፡፡
የጃፓን ገዢ መደብ በ1868 ዓ.ም ይህን አቋም ወስዶ፤ ‹‹ሁሉም ነገር ወደ ልማት›› ብሎ መረባረብ በጀመረ ጊዜ፤ ምናልባት ከጃፓን ቀድመው የአውሮፓን ስልጣኔ መቅሰሙ አስፈላጊ መሆኑን የተረዱት አፄ ቴዎድሮስ፤ መቅደላ አፋፍ ላይ ከእንግሊዝ ወራሪ ጦር ጋር ባልሞት ባይ ተጋዳይነት ፍልሚያ ገጥመው፤ እርሳቸው አጥብቀው ይመኙት የነበረውን ጥበብ ከታጠቀ ኃያል ጦር ጋር ተናንቀው፤ ሞታቸውን ከመንጋጋው መንጭቀው፤ እዚያች አምባ ላይ ወደቁ፡፡ አፄ ቴዎድሮስ በሞቱ ዓመት 1868 ዓ.ም (እኤአ)፤ ጃፓን አውሮፓውያን ሳያስቡት ሹልክ ብላ በማምለጥ የኢንዱስትሪ አብዮት ማካሄድ ቻለች፡፡ አውሮፓውያን ሳይገምቱት፤ የኢንዱስትሪ አብዮት ማካሄድ የቻለች ብቸኛዋ የቢጫ ህዝቦች ሐገርም ለመሆን በቃች፡፡
አፄ ቴዎድሮስ፤ ኢትዮጵያ የምዕራቡን ስልጣኔ በፍጥነት ካልያዘች፤ ነፃነቷን ጠብቃ እንደ ሐገር መቆየት እንደማትችል ተረድተውት ወይም ተገልጦላቸው ነበር፡፡ እናም አጥብቀው የሚመኙትን ስልጣኔ ለማግኘት ዕረፍት አጥተው ሲማስኑ እና ጥበብን በመሻት አውሮፓውያንን ደጋግመው ሲማፀኑ እናያለን፡፡ ንጉሱ በነበራቸው ከፍተኛ ጉጉት እየተሳቡ፤ ሳያስቡት ከእንግሊዝ ጋር ጦር የሚያማዝዝ ችግር ውስጥ ገቡ፡፡  
አፄ ቴዎድሮስ፤ ሐገሪቱ ዙሪያዋን በጠላት የተከበበች ሆኖባቸው፤ እንደ ጃፓን የራሳቸውን ሰዎች ወደ አውሮፓ በመላክ የምዕራቡን ስልጣኔ ለመቅሰም አልቻሉም፡፡ ለእንግሊዝ ንግስት በፃፉት ደብዳቤ፤ የሐገራቸውን ሰው ወደ አውሮፓ ለመላክ እንዳልቻሉ ጠቀሰው፤ ‹‹የእኔን ሰዎች እንዳልክም ጠላት አላሳልፍ አለኝ›› በማለት፤ እንግሊዝ ሙያተኞችን እንድትልክላቸው ይጠይቁ ነበር፡፡ ለህዝባቸው ጥበብን የሚያካፍል ሙያተኛ እንዲልኩላቸው የእንግሊዝ እና የፈረንሳይ መንግስታትን ተማፅነዋል፡፡ ሆኖም፤ ከእንግሊዝም ሆነ ከፈረንሳይ  ቀና ምላሽ አጡ፡፡ እንደ ጃፓኑ ንጉስም፤ የመኳንንቱን እና የህዝቡን ድጋፍ ማግኘት አልቻሉም፡፡
መኳንንቱን እና ህዝቡን በዓላማው ዙሪያ ለማሰለፍ ያልቻለው፤ እንዲሁም ዙሪያውን በጠላት የተከበበው መንግስታቸው፤ እንደ ጃፓን የአውሮፓን ስልጣኔ አይቶ የሚመጣ ቡድን ወደ አውሮፓ መላክ የሚችል አልነበረም። እናም ኢትዮጵያ እንደ ጃፓን የሥልጣኔ ምድር የሆነውን የአውሮፓ አህጉር አይታ መመለስ የምትችልበት ዕድል አላገኘችም፡፡ በየአካባቢው ያለው ሽፍታ ከሚጥለው አደጋ በተጨማሪ፤ ቱርክ እና ግብፅ፤ የኢትዮጵያ መልዕክተኞች በሰላም ግዛታቸውን አቋርጠው እንዲሄዱ  ለማድረግ ፈቃደኞች አልነበሩም። ስለዚህ የኢንዱስትሪ አብዮት፤ ኢትዮጵያን እንዳማራት ቀረ፡፡ ለዚህ መጣጥፍ መነሻ ያደረግኩት ጥናት አለ፡፡ ኖራ ኬ. ሁቨር (NORA K. HOOVER) የተባሉ አንድ ምሁር፤ በፍሎሪዳ ስቴት ዩኒቨርስቲ፤ የሥነ ጥበባት እና የሳይንስ ኮሌጅ፤ ለሦስተኛ ድግሪ (PhD) ትምህርታቸው ማሟያ አድርገው ባቀረቡት፤ ‹‹የቪክቶሪያ ዘመን የጦርነት ዘገባ›› በተሰኘ ጥናታቸው፤ የጦርነት ዘገባ እንደ አንድ የጋዜጠኝነት የሥራ ዘርፍ ብቅ ያለው፤ እንግሊዝ አፄ ቴዎድሮስን ለመውጋት ባደረገችው ዘመን መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡      በእንግሊዝ የመቅደላ ዘመቻ ላይ ያተኮረውን ይህን ጥናት አግኝቼ ባነበብኩ ጊዜ፤ ከመነሻ የጠቀስኩት ‹‹የታሪክ መጨረሻ እና የመጨረሻው ሰው›› የሚለው የፍራንሲስ ፉኩያማ የመፅሐፍ ርዕስ የአፄ ቴዎድሮስን ታሪክ በትክክል ለመግለፅ የሚያስችል ሆኖ ተሰምቶኝ አነሳሁት፡፡ ከዚህም አልፎ፤ የአፄ ቴዎድሮስን ታሪክ በጥሞና ሳስተውል፤ በእኛ ዘመን እና በአፄ ቴዎድሮስ ዘመን መካከል ጥሩ ንፅፅር ለመፍጠር የሚያስችሉ የተለያዩ ጉዳዮችን እያሰብኩ ተብሰልስያለሁ። የኢትዮጵያ ታሪክ፤ በማለፊያ ደራሲ እንደ ተነደፈ ድንቅ የተውኔት ሥራ ሴራ ትልሙ በጉልህ ወጥቶ፤ በጡዘት እና ልቀት ተሰናስሎ የተደራጀ ትረካ በማየቴ፤ ለጋዜጣው አንባቢ ለመናገር ሳይሆን ለራሴ የታሪካችንን ውል በደንብ ለመረዳት በማሰብ መፃፍ ጀመርኩ፡፡ እናም፤ ታሪካችንን በደንብ ለመረዳት የሚያግዝ ምቹ ፉካ አግኝቼ፤ በዚያ እየተደነቅኩ መፃፉን ተያያዝኩት፡፡
የከሸፈ ጥረት
ጥንት ጀምሮ ከአውሮፓም ሆነ ከእስያ የተለያዩ ግንኙነቶችን እንዳትመሰርት እንቅፋት የነበሩት ምክንያቶች ለረጅም ዘመናት ሳይወገዱ ቆይተዋል። ግብፅ፤ በድሮው ዘመን የኢትዮጵያ መልዕክተኞች ወደ አውሮፓ እንዳይሻገሩ ስታደርግ ኖራለች፡፡ ይህን በማድረግ ቢያንስ-ቢያንስ 70 በመቶው የውሃ ሐብታችን በአባይ ተፋሰስ የሚገኝ በመሆኑ በዚህ ሐብታችን እንዳንጠቀም አድርጋን ቆይታለች፡፡  በነገራችን ላይ፤ አሁን የግብፅ መንግስት እና ህዝብ እያሳዩት ላሉት የተለየ ዝንባሌ አክብሮቴ ክፍ ያለ መሆኑ እንደተጠበቀ፤ ግብፅ መንገድ መከልከል የማይቻልበት ዘመን ከመጣ በኋላም፤ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ የፋይንስ ምንጭ ሊሆኑ ከሚችሉ አበዳሪ ተቋማት እና ሐገራት በር ላይ ቆማ እንደ ውሻ እየተናከሰች አላሳልፍ ብላ ቆይታለች፡፡ ኢትዮጵያ የድረሱልኝ ጥሪም ሰሚ እንዲያጣ በማድረግ ‹‹የተሳካ ሥራ›› ሰርታለች፡፡
የታሪክ ፀሐፊዎች እንደሚሉት፤ በጥንታዊው የኢትዮጵያ ታሪክ ለታየው ስልጣኔ ምንጭ የነበረው እና በቀይ ባህር አካባቢ ለነበረው ንግድ ዋነኛ ሞተር ሆኖ ያገለግል የነበረው የምፅዋ ወደብ ነው፡፡ ይህ ወደብ በኢትዮጵያ እጅ በነበረበት ጊዜ፤ ሐገሪቱ ከዓለም ጋር የጠበቀ ትስስር እንደነበራት የሚገልፁት እነኚህ የታሪክ ፀሐፊዎች፤ የምፅዋ ወደብን በእጇ ማቆየት በተሳናት እና በተለያዩ ኃይሎች በተነጠቀች ጊዜ፤ ከዓለም ተነጥላ ኋላ ቀር ሐገር እየሆነች እንደመጣችም ይናገራሉ፡፡
ስለዚህ፤ በጠላት ዓይን በሚመለከቷት ጎረቤቶች ዙሪያዋን የተከበበችው ኢትዮጵያ፤ ከሥልጣኔ ማማ ወርዳ የድህነት እና የኋላ ቀርነት ማጥ ውስጥ ተዘፈቀች፡፡ ነባሩ የሐገሪቱ የአስተዳደር ህግ እና ስርዓት ፈርሶ፤ በምትኩ ስርዓት አልበኝነት ነገሰባት፡፡ የህግ እና ስርዓት እጦቱ ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰው ደግሞ በዘመነ-መሳፍንት ወቅት ነበር፡፡ ለብዙ ዘመናት፤ ሐይማኖታዊ እና ፖለቲካዊ መነሻ ባለው የእርስ እርስ ጦርነት እየደቀቀች፤ ህዝቧም ኋላ ቀር እና ድሃ ሆኖ ዘመናትን ገፋ፡፡
በዚህ ሁኔታ፤ የዘመናዊት ኢትዮጵያ መስራች ከሚባሉት አፄ ቴዎድሮስ ዘመን የደረሰችው ኢትዮጵያ፤ በእሳቸው ዘመን፤ በእኔ እበልጥ - እኔ እበልጥ ይፋለሙ በነበሩ መሣፍንት ጦርነት በእጅጉ የተዳከመች እና እንደ ተራበ አንበሳ አፍሪካን በቅኝ ግዛት ለመቀራመት ባሰፈሰፉ ኃያላን መንግስታት የተከበበች ሐገር ሆነች። ታዲያ ለዘመናዊት ኢትዮጵያ ፈተና የነበሩት ችግሮች፤ በቅርፅ ወይም በመከሰቻ መልክ የተለያዩ መስለው ቢቀርቡም፤ በመሠረታዊ ይዘት ሳይለወጡ ሐገሪቱን ሰንገው እንደያዟት እስከ ሃያኛው ምዕተ ዓመት ማብቂያ ድረስ ዘልቀዋል፡፡
አንዳንዴ፤ ተፈጥሞ ለመናገር የማያመች ነገር ሲያጋጥመን፤ ‹‹እንዳልምል ይህን አድርጎልኛል ወይም እንዲህ ሆኗል›› እንደምንለው፤ በጥቅል መናገርን የሚከለክሉ በዓይን የሚታዩ የታሪክ ቅርሶች ቢኖሩም፤ ያለፈውን ‹‹ሻመት›› (ጋዜጠኞች ‹‹ምለኒየም›› ወይም ሺህ ዓመቱን (ሻመቱን) ምዕተ ዓመት አሉት፤ እናም በስህተት ሁሉም የMGDን ግቦችን ‹‹የምዕተ ዓመቱ ግቦች›› ይላል)፤ ያለፈውን ‹‹ሻመት›› እንደ ገደል ናዳ ከሥልጣኔ አምባ ቁልቁል እየተንከባለልን ወርደን፤ ከውርደቱ የመጨረሻ ዝቅታ የደረስነው፤ ዘመነ-መሣፍንት በምንለው የታሪካችን ምዕራፍ ነው፡፡ አፄ ቴዎድሮስ፤ የቁልቁለት ጉዞውን ሊገቱት ባይችሉም፤ ቢያንስ ቁልቁል እየተጓዝን መሆኑን በመረዳት፤ የሚያስቆጭ እና ልብን የሚያደማ፤ እንደ ተውኔት ለሚመለከተው ሰው አሳዛኝነቱ ጎልቶ የሚታይ ትራጀዲያዊ ፍፃሜ ያለው ጥረት አድርገዋል። አፄ ቴዎድሮስ፤ ‹‹ኤዲፐስ ንጉስ›› በተሰኘው ተውኔት ውስጥ እንደምናየው ያለ እንቆቅልሽ ገጥሟቸው ነበር፡፡
እናም፤ ታሪክ እያንከባለለ አምጥቶ ከፊታቸው የጣለውን ያን እንቆቅልሽ እንዲፈቱ ሲጠየቁ፤ ልዩ ችሎታ እንዲላበስ እንደ ተደረገ ጀግና ገፀ ባህርይ፤ ከዘመኑ ማህበረሰብ ላቅ ያለ አመለካከት እና መንፈስን ተላብሰው እንቆቅልሹን ለመፍታት ሲክሩ እናያለን፡፡
አፄ ቴዎድሮስ፤ የብዙ ታሪክ ፀሐፊዎችን እና የሐገራችንን ደራሲያን ልብ መማረክ የቻሉት በታላቅ ራዕያቸው እና ለህዝባቸው በነበራቸው ፍቅር የተነሳ ነበር። አፄ ቴዎድሮስ የሐገሪቱ አንድነት ማጣት፣ የተንሰራፋው ድንቁርና፣ መሣፍንቱ የሚያደርሱት በደል፣ የህዝቡ ሞራል መውደቅ፣ በዙሪያቸው ያንዣበበው ሐገራዊ ህልውናን የሚያጠፋ አደጋ በሙሉ ታይቷቸው ነበር። ሐገሪቱ ይህን ከባድ ፈተና ማለፍ የምትችለው በአንድ ብቸኛ መንገድ መሆኑንም ተረድተው ነበር፡፡ በአጭሩ፤ መንገዱ ሥልጣኔ እና ጥበብ በሚል ሊገለፅ ይችላል፡፡
ከፍ ሲል የጠቀስኳቸው የጋዜጠኞችን የጦርነት ዘገባ አቀራረብ ታሪክን ለመመርመር የሞከሩት ምሁር፤ በአፄ ቴዎድሮስ ታሪክ ውስጥ ጉልህ ምዕራፍ የያዘውን እና ሰባት ወራት የፈጀውን የመቅደላ ዘመቻ መሠረት አድርገው ካቀረቡት ጥናት የተረዳሁት ነገር፤ አፄ ቴዎድሮስ፤ ችግሩ እና መፍትሔ ፍንትው ብሎ ቢታያቸውም፤ መፍትሔ ካሉት ነገር የሚያደርሳቸውን ጎዳና መለየቱ አልተሳካላቸውም፡፡
ነገሩን፤ ከግል ባህርይ እንከን የመጣ ውድቀት አድርጎ ለማየት የሚገፋፉ ጉዳዮች ብዙ ቢሆኑም፤ እንደኔ አስተሳሰብ የወቅቱ ሐገራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ክስተቶች፤ በ‹‹ፈላስፋ ንጉስ›› ብህልነት እና አስተዋይነት ላይ የማፌዝ ብቃት የነበራቸው ከባድ ችግሮች መሆናቸውን መዘንጋት አይኖርብንም፡፡ ሐገራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ክስተቶቹ፤ ድንቃይ እንደሚሉት የተውኔት ዘውግ፤ በሰው ህይወት የመዘባበት ብቃት የያዙ ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡
የሆነ ሆኖ፤ ፕላውዴን ስለ አፄ ቴዎድሮስ ሰብዕና እና የመሪነት ባህርይ ያለውን ግምገማ በገለፀበት ደብዳቤ፤ ‹‹...ምናልባት አንዳንድ ሐሳቦቻቸው ላይ ችግር ሊስተዋል ይችላል፡፡ አንዳንዶቹም ተፈፃሚ ሊሆኑ የማይችሉ ከንቱ ቀዠቶች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ሆኖም፤ ከሐበሻ የድንቁርናና የልጅነት ደመና ውስጥ ብቅ ያለው ይህ ሰው፤ አንዳች ረዳት እና መካሪ ሳይኖረው ብዙ ትላልቅ ጉዳዮችን ማከናወን የቻለ ሰው ነው፡፡ አሁንም ሊሰራቸው የሚያስባቸው ትላልቅ ዕቅዶች እና ውጥኖች ያሉት በመሆኑ፤ ሰውዬው የተለመደ ተራ ሰብዕና ያለው አይደለም›› በማለት ፅፎ ነበር፡፡      (ይቀጥላል)

Published in ህብረተሰብ

የኢህአዴግ ካድሬዎች ከባድ ግምገማ ይጠብቃቸዋል
“የጎረቤት አገራት የተቃውሞ ሰልፍ እናዘጋጃለን”

     የሆነስ ሆነና የጋዜጣው ዜና ምንድነው? የጦቢያ ልጆች አሜሪካንን በመውደድ ከዓለም በሶስተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኙ በጥናት መረጋገጡን የሚጠቁም ዘገባ ነው፡፡ ታዲያ አሜሪካንን መውደድ ምን ችግር አለው ልትሉ ትችላላችሁ፡፡ አያችሁ----የአሜሪካ አፍቃሪ ሆነን Top 3 ውስጥ ገባን ማለት፣ ቀንደኛ የኒዮሊበራሊዝም አቀንቃኝ ሆንን ማለት ነው፡፡ (ኒዮሊበራሊዝምና አብዮታዊ ዲሞክራሲ ደግሞ ሆድና ጀርባ ናቸው!)
እኔ የምለው ግን----ላለፉት 24 ዓመታት ከቻይና ልዩ የቴክኒክ ድጋፍ የሚደረግለት የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ርዕዮተ ዓለም በገነነበት አገር፣ (ወደፊትም እኮ መግነኑ ይቀጥላል ተብሏል!) እንዴት ነው የአበሻ ዘር የኒዮሊበራሊዝም አቀንቃኝዋን (አሜሪካን ለማለት ነው!) በመውደድ ከዓለም 3ኛ ነው የሚባለው? (አገሪቱም ህዝቡም እንቆቅልሽ ሆነው አረፉት!) ከምሬ እኮ ነው----ህዝብና መንግስት አይደማመጡም ማለት ነው? (ከመቼ ወዲህ እንዳትሉኝ!) ይሄ እኮ ለሰሚውም ግራ የሚያጋባ ነው፡፡ መንግስት በአብዮታዊ ዲሞክራሲ ነው የምመራው ይላል፤ የሚመራው ህዝብ ግን የለየለት የኒዮሊበራሊዝም አቀንቃኝ ሆኗል፡፡ (ደግነቱ  ምርጫው በድል ተጠናቋል!)  
እስቲ በመሃል ደግሞ ለዶክትሬቱ ጥናት ለመስራት አማራ ክልል ሰንብቶ የመጣ ወዳጄ ያወጋኝን ላውጋችሁ፡፡ ወዳጄ እዚያው ጥናቱን በመስራት ላይ ሳለ፣ አንድ የሚያከብራቸው ምሁር ይደውሉለትና፤
 “ጎረምሳው፤ በሰላም ነው  የጠፋኸው?” ሲሉ ይጠይቁታል፡፡
ወዳጄም ጨዋታ አምሮት፤ “ምን ባክዎ---የአገሪቱን ችግር ለመፍታት ጥናት እያካሄድኩ ነው” ሲል ይመልስላቸዋል፡፡
ምሁሩም አንዴ ሳቃቸውን በረዥሙ ለቀቁትና፤ “አንተ ዝም ብለህ መመረቂያህን ሥራ ባክህ---እኛ ኢህአዴግን 100 ፐርሰንት የመረጥነው እኮ የአገሪቱን ችግር ይፈታልናል ብለን ነው!” ብለው በሳቅ አፈረሱኝ ሲል አወጋኝ (እኔም ሳቄን ለቀቅሁት!)
  አሁን ወደ ጀመርነው አጀንዳ እንመለስ፡፡ በነገራችን ላይ (ይቅርታ አድርጉልኝና) ዝም ብዬ ስጠረጥር  --ህዝቡ ብቻ ሳይሆን አንዳንድ የኢህአዴግ አባላትም ልባቸው ከቻይና ይልቅ ለአሜሪካ የሚያደላ ይመስለኛል፡፡ (አይፈረድባቸውም!) አያድርገውና አንድ ቀን ፓርቲያቸውን ቢያኮርፉ ወይም ቢያኮርፋቸው  የምታስጠጋቸው አሜሪካ እንጂ ቻይና አይደለችም፡፡ ተሳስቶ ቻይናን የፖለቲካ ጥገኝነት የጠየቀ ባለሥልጣን አለቀለት፡፡ በቻይንኛ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ተሃድሶ ይሰጠውና በክብር ለመጣበት አገር መንግስት ተላልፎ ይሰጣል፡፡ (ደግነቱ ማንም እግሩን ወደ ቻይና አያነሳም!)
 ኢህአዴግ እንዳይሰማኝ እንጂ አሜሪካን በመውደድ የተሰጠን ደረጃ በደንብ ተጭበርብሯል (ኦባማ ሲመጡ ቅሬታዬን አሰማለሁ!) አሁን ማን ይሙት---- የፊሊፒንሶች ፍቅር ከእኛ አይሎ ነው ለእነሱ 1ኛ ደረጃ የተሰጠው? (“አያውቁንም” አለ ዘፋኙ!) እንዴ የጦቢያ ባለሀብት በሉት ባለስልጣን፣አርቲስት በሉት አትሌት…ሚስቱ ስታረግዝ የሚሽቀዳደመው እኮ የአሜሪካንን ቪዛ ለማግኘት ነው (ልጁ አሜሪካ እንዲወለድለት!) ሳይደርሰን ቀርቶ እንጂ የአሜሪካ ዲቪን ያልሞላ የጦቢያ ልጅ እኮ የለም፡፡ ታዲያ ከዚህ በላይ አሜሪካንን መውደድ አለ እንዴ?! (ፊሊፒንሳውያንማ በተዓምር አይደርሱብንም!)
በነገራችን ላይ ለአሜሪካ ያለን ፍቅር እኮ ዛሬ የተፈጠረ አይደለም፡፡ በደርግ ዘመንም ቢሆን ሶሻሊስታዊ ሥርዓት በአገሪቱ ላይ እናነግሳለን ብለው እርስ በእርስ የተፋጁት የዚያ ትውልድ አባላት… የማታ ማታ የተሰደዱት እኮ ሩሲያ ወይም ኩባ አልነበረም፡፡ አሜሪካ እንጂ! የሚገርመው ያኔም እንዳሁኑ ደርግ ሶሻሊዝምን ሲያቀነቅን፣ ሰፊው ህዝብ በልቡ ቀንደኛ የኢምፔሪያሊዝም አቀንቃኝ ነበረ (መንግስትና ህዝብ ሲሸዋወድ እኮ ነው የኖረው!)
የደርግ፣ ታሪክ ስለሆነ እንተወውና ወደ ዛሬው እንመለስ፡፡ እናላችሁ---እንደ እኔ ከሆነ ለህዝባችን የኒዮሊበራሊዝም አቀንቃኝ መሆን ዋነኛ ተጠያቂው ራሱ ኢህአዴግ ነው፡፡ ለምን መሰላችሁ? ፓርቲው ላለፉት 24 ዓመታት እንዴት አብዮታዊ ዲሞክራሲን በእኛ ውስጥ ማስረፅ አቃተው? (የኢህአዴግ ካድሬዎች 1ለ5 ብቻ ነው እንዴ የሚያውቁት?) ከምሬ እኮ ነው … ምድረ ካድሬ ታሪካዊ ግምገማ ያስፈልገዋል፡፡ (ህዝቡን ግን በተሃድሶ ጠበል መሞከር ነው!)
እኔ የምለው ግን--- ኢትዮጵያውያን ቻይናን በመውደድ ከዓለም ስንተኛ የምንሆን ይመስላችኋል? (የቀለበት መንገዳችን ባለውለታ መሆኗን እንዳትዘነጉ!) በዚያ ላይ ገደኛ ናት (ተዓምረኛው ባለ 2 ዲጂት ዕድገት የመጣው እኮ ቻይና ጦቢያን ከረገጠች በኋላ ነው!) እንደው ለጠቅላላ ዕውቀት ያህል---በመላው ዓለም እነማን ቻይናን እንደ ነፍሳቸው እንደሚወዱ፣ እነማን ደግሞ ዓይንሽን ላፈር እንደሚሏት ቢጠና ጥሩ ነው። (አሜሪካ ስፖንሰር ካደረገች እንጂ ቻይናማ ንክች አታደርገውም!)
አኔ የምላችሁ----ለውጭ ዜጎች የተቃውሞ ሰልፍ በክፍያ ተጀመረ እንዴ? ባለፈው ሳምንት ኤርትራውያን በአዲስ አበባ ያደረጉትን ሰልፍ አይቼ እኮ ነው፡፡ (በዶላር ከሆነ ያዋጣል!) በተለይ አፍሪካ ውስጥ ከሆነ የደራ ገበያ አለው፡፡ ይኸውላችሁ አብዛኞቹ የአፍሪካ መንግስታት አምባገነን ስለሆኑ እንኳን የተቃውሞ የድጋፍ ሰልፍም አይፈቅዱም። ያኔ የአፍሪካ ተቃዋሚዎች ተራ በተራ ወደ ኢትዮጵያ በመደወል፣ ለሚፈልጉት ቀን ሰልፉን ቡክ ያስደርጋሉ፡፡ (ዘመናዊ ማኔጅመንት ግን ይፈልጋል!) በአገራችን ተቃዋሚዎች ለምዶብን መስቀል አደባባይን ሲጠይቁ፣ እየለማ ነው ወይም ሌላ ቦታ ምረጡ፣ በሚቀጥለው እንጂ በዚህኛው ሳምንት አይቻልም ---- ምናምን አይሰራም (ይሄ እኮ ፖለቲካ ሳይሆን ቢዝነስ ነው!)   
የኤርትራውያንን የአዲስ አበባ የተቃውሞ ሰልፍ የተመለከቱ አንድ የአገራችን የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር ምን አሉ መሰላችሁ? “ከዚህ በኋላ እኛም ጋና ወይም ቦትስዋና ሄደን የተቃውሞ ሰልፍ እናደርጋለን” (“ባቄላ ቀረ ቢሉ--” የምትለዋን ተረት የሚተርቱ ኢህአዴጎች አይጠፉም!) በነገራችን ላይ ኤርትራውያን በጣም ነው ያሳዘኑኝ (በየቀኑ 5ሺ ኤርትራውያን ይሰደዳሉ ነው የተባለው?) እንደ እነሱ በመሪው የተጭበረበረና የተካደ ህዝብ ያለ አይመስለኝም፡፡ መጀመሪያ ላይ እኮ --ወዲ አፈወርቂ የእያንዳንዱ ኤርትራዊ ጀግና (Hero!) ነበሩ፡፡ ዛሬ ከ24 ዓመት በኋላ ግን--- ኤርትራውያን የአገራቸውን መሪ በመጥላት ከዓለም ቀዳሚ ህዝቦች ሳይሆኑ አይቀሩም! (በኤርትራ ነጻነትም ባርነትም አልተቻለም!) አንጋፋው ኢትዮጵያዊ ምሁር ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም እንዲህ ያለነውን ይመስለኛል - “መክሸፍ” የሚሉት፡፡  (የራሳችን ምሳሌ አጥቼ እንዳይመስላችሁ!)

ኢትዮጵያ ውስጥ መኪና፣ አውሮፕላን፣ ሮኬት፣ የኒኩለር ማበልፀጊያ አይሠራም አትበሉ። ዓለም እኮ
ብዙ አልቀደመችንም። ቢበዛ የሀምሳ ወይም የመቶ ዓመት እርምጃ ነው ከፊታችን ያለችው። ----

   ይህን አጭር መጣጥፍ ለመጻፍ ያነሳሳኝ ባለፈው እሁድ በኢቢሲ የመዝናኛ ፕሮግራም የተመለከትኩት በአንድ ኢትዮጵያዊ የተደረገ የመለስተኛ አውሮፕላን ሥራ ሙከራ ነው።
በብዙ የፈጠራ ሙከራዎች በተለይ ደግሞ በአውሮፕላን፣ በሮኬት እና በኒኩለር ማበልፀጊያ ሥራዎች የበርካታ ኢትዮጵያዊያን አመለካከት አይቻልም የሚል ነው። በዚህ ጐራ ውስጥ የሚመደቡት የተማሩ የሚባሉ ኢትዮጵያዊያን ጭምር መሆናቸው ደግሞ ሁሌም የሚያስገርመኝ ነገር ሆኖ ቆይቷል። ዘመን ይጥላል፤ ዘመን ያነሳል። ባንድ ወቅት ኢትዮጵያ ከሦስቱ የዓለም ኃያላን መንግሥታት አንዷ ነበረች። በአንድ ወቅትም ግብጽ ኃያል ነበረች። ፐርሺያም፣ ግሪክም፣ ሮማም በዘመናቸው ኃያል ነበሩ። እንግሊዝ፣ ፖርቱጋል እና ስፔን ኃያል ነበሩ። የአሜሪካ ኃያልነት አሁንም ለጥቂት ጊዜ ይቀጥላል። ከአሜሪካ ጐን ለጐን ጃፓን ወደ ታላቅነት ተሸጋግራለች። አሁን ደግሞ ቻይና ወደ አንደኛነት እየተንደረደረች ነው። የቻይና ታላቅነት ከአንድ መቶ ዓመታት ጀምሮ ሲተነበይ የቆየ ነው። የያኔ ነቢያት ራእይ እንደ ቅዠት ተወስዶ ነበር። አሁን ግን እውን ሆኗል። በቻይና የትልቅነት ትንቢት የተሳለቁ አሁን አፍረዋል።
የእሥራኤል ምጽአት እና ትልቅነት በየባህሉ ሲተነበይ ቆይቷል። በዓለም ካርታ ላይ እንኳ ምልክት ያልነበራት እሥራኤል አሁን አንቱ የተባለች አገር ሆናለች። አስትሮሎጂ ጥንታዊ እና ድንቅ የሆነ ጥበብ ነው። አንዳንዶች የሳይንስ ሁሉ አባት ነው ይሉታል። ይኸ የከዋክብት ሳይንስ የበርካታ ሀገራትን ውድቀትና እድገት ተንብዮአል።
የዛሬ አሥራ ሁለት ሺህ ዓመት (በአስር ሺህ ዓመተ ዓለም) ሊዮ ሀገሮች ተነስተዋል። እነ አትላንቲስን የመሰሉ አኳሪየስ ሀገሮች ጠፍተዋል። የዓለም ዐቢይ ሥልጣኔ የሚጀምረውና የሚያበቃው በአኳሪየስ ኮከብ ነው። በዓለም ላይ አኳሪየስ የሆኑ አገሮች ጥቂት ሲሆኑ በቁጥር ስድስት ናቸው። እነዚህም ራሺያ፣ ስዊድን፣ ፖላንድ፣ እሥራኤል፣ ፐርሺያ (ኢራን) እና ኢትዮጵያ ናቸው።
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሱት ሦስቱ ሰብአሰገሎች (አስትሮሎጀርስ) የፖላንድ፣ የፐርሺያ እና የኢትዮጵያ ጠቢባን እንደሆኑ ይታመናል። ከስድስቱ አኳሪየሳዊ ሀገራት ውስጥ ሙሉ በሙሉ አኳሪየስ የሆኑት ፖላንድ እና ኢትዮጵያ ናቸው። ራሺያ ስኮርፒዮነት፣ እሥራኤል ስኮርፒዮነት እና ቶረስነት፣ ፐርሺያ ቶረስነት፣ ስዊድን ሳጁታሪየስነት የተጫናቸው ስለሆኑ መቶ በመቶ አኳሪየስ የሆኑ አገሮች አይደሉም። ፖላንድ እና ኢትዮጵያ የሚበላለጡት በአሁኑ ታላቅ የአኳሪየስ ዘመን ዋናው ተራ ወይም ጽዋ የኢትዮጵያ መሆኑ ብቻ ነው። በሚቀጥሉት መቶ ዓመታት ውስጥ ኢትዮጵያ በዋናነት፣ ፖላንድ ደግሞ በተከታይነት የዓለም ቁንጮ እንደሚሆኑ ይጠበቃል። አሁን ኢትዮጵያ ላይ እናትኩር።
የኢትዮጵያ ኮከብ አኳሪየስ ነው። ይኸ እኔ እንኳን እስከማውቀው የዛሬ ሁለት ሺህ ዓመት በፒቶሎሚ ቴትራቦሊስ የተመዘገበ ነው። በየጊዜውም የተነሱ ሰብአሰገሎች መዝግበውታል። በእኛ ዘንድ በጥቂቱ  ከዛሬ አስራ አራት ሺህ ዓመት በፊት ይታወቃል። በሀገራችን ዐውደነገሥትም ነገሩ ስለመታወቁ ፍንጮች አይቻለሁ።
ዘመንፈስ ቅዱስ አብርሃ ባጠናቀሩት ሐተታ መናፍስት ወዓውደነገሥት በመጨረሻው አስራ ሁለት ገፆች የአስራ ሁለት ሀገራት ኮከብ ተዘርዝሯል። ሮም ሐመል (ኤሪስ)፣ ቱርክ ሠውር (ቶረስ)፣ ምስር (ግብጽ) ገውዝ (ጄሚናይ)፣ ዠንዲ ሸርጣን (ካንሰር)፣ ካቤል አሰድ (ሊዮ)፣ ኤለለንጅ ሰንቡላ (ቪርጐ)፣ አልኸዠሬ ሚዛን (ሊብራ)፣ ህንድ ዓቅራብ (ስኮርፒዮ)፣ ሰገድ ቀውስ (ሳጁታሪየስ)፣ አልቡም ጀዲ (ካፕሪኮርን)፣ ሐቢሽ (ኢትዮጵያ) ደለዊ (አኳሪየስ)፣ እንግልጣር (እንግሊዝ) ደግሞ ፓይሰስ ተብላለች። እዚህ ላይ በተለይ ኢትዮጵያ በደለዊነት ወይም በአኳሪየስነት መጠቀሷን ልብ ይሏል።
አኳሪየስ የፈጠራ እና የፍጥረት መነሻ ነው። የሳይንስ ንፋስ ወዴትም ይንፈስ ወዴት ኢትዮጵያ የሰው ልጅ መጀመሪያ የተፈጠረባት፣ የሥልጣኔ መሠረቶች ሁሉ የተጣሉባት አገር እንደሆነች አሁን ብዙም ጥርጥር ያለው ነገር አይደለም።
እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ የሴማዊ ቋንቋዎች ምንጭ መካከለኛው ምስራቅ ተደርጐ ሲወሰድ ቆይቷል። የሀገራችን መምህራንም ከፈረንጅ የሰሙትን እያስተጋቡ የኢትዮፒክ (ሳባ) ፊደል ከወደየመን እንደመጣ ሲናገሩና ሲጽፉ ቆይተዋል። የቅርብ ጊዜ ምርመራዎች ግን የፊደላቱም ሆነ የቋንቋው ምንጭ ኢትዮጵያ እንደሆነች በግልጽ አመላክተዋል።
በግልጽም ሆነ በስውር በተጻፉ መዛግብት ደግሞ የአስትሮሎጂ ሳይንስ ራሱ ከኢትዮጵያ እንደሆነ ተነግሯል። የሮኬት፣ የኒኩለር፣ የበረራ እና መሰል ዕውቀቶችም ምንጫቸው ኢትዮጵያ ነች። ይኸ መቼም ከንቱ ግብዝነት ነው የሚመስለው። እስከ አለፉት አስር ዓመታትም ድረስ የኔ አመለካከት እንደዚያ ነበር።
የመጽሐፍ ቅዱሱን ሙሴ ከኢትዮጵያ ጋር ማቆራኘት አጉል ጀብደኝነት አይደለም። ሙሴ የሀይማኖት መሪ ብቻ አልነበረም። ሙሴ የታላቅ ጥበብ ባለቤት የነበረ ኢትዮጵያዊ ነው። ከቃል ኪዳኑ ታቦት ጋር ተጣምሮ መላቅጡ ጠፋብን እንጂ ሙሴ ከኢትዮጵያዊያን ጋር በመሆን ከሌላ ዓለማት ጋር የሚነጋገርበት ቴክኖሎጂ (ራዲዮ) ሠርቷል። ይህ ራዲዮ የሳባ ንግሥት የተባለችው ኢትዮጵያዊት ወደ ኢትዮጵያ ይዛው ተመልሳለች። ይህ ልዩ ራዲዮ ከቃል ኪዳኑ ታቦት ጋር አንድ አይደለም። የቃል ኪዳኑ ታቦት የመጣው በሳባ ልጅ ነው። ቀዳማዊ ምኒልክ የሰለሞን ልጅ ነው የሚባለው መነሻው ልክ ቢሆንም መድረሻው ግን ተረት ነው። የሱ ታሪክ ሌላ ነው። [በመጪዎቹ ሠላሳ ዓመታት ውስጥ ይህ ምስጢር ይገለጣል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።] ሁሉ ነገር ከውጪ ካልመጣ ለምን ትልቅ እንደማይመስለን አይገባኝም። አሁን እንደሚመስለኝ ኢምፖርት የማናደርገው ፓትርያርክ ብቻ ሳይሆን አይቀርም።
የዓለም ጊዜ በአስራ ሁለት ታላላቅ ዘመናት (Great Ages) ይከፈላል። አንዱ ዙር በአማካይ ሀያ ስድስት ሺህ ዘመን ይወስዳል (ቀጥታ ቁጥሩን ለጊዜው እንተወው)። በዚህ ስሌት የአኳሪየስ ዘመን በ26ሺህ ዘመን ይከሰታል። በዚህ መሐል የአኳሪየስ ዋልታዊ ኮከብ የሆነው ሊዮ በ13ኛው ሺህ ይወጣል።
አኳሪየስ ታላቅ፣ ሊዮ ታናሽ ነው። በአኳሪየስ ዘመን የሚታይ ትንቢት በሊዮ ዘመን ከፊሉ ይወጣል። የዛሬ 12 ሺህ ዘመን ገደማ (10,000 ዓመተ ዓለም) በምድራችን ታይቶ የነበረው ታላቅ የሳይንስና ቴክኖሎጂ እመርታ በሊዮ ዘመን የሆነ ነው። በዚህ ጊዜ አሁን እንደ ተረት የምትጠቀሰው የአትላንቲስ አህጉር ከነሥልጣኔዋ ጠፍታለች። ከዚህችም አህጉር እየተቀነጨቡ የደረሱንን ጥበባት የቃረሙ ሊቃውንቶቻችንን እንደ ጠንቋይ እና አስማተኞች ስናይ ቆይተናል። በአሁኑ ዘመን እየታዩ ያሉ የሳይንስ እመርታዎች ሁሉ የአትላንቲስ ዘመን የሁለት በመቶ ያህል ብቻ ቅጂዎች ናቸው። ኢትዮጵያ እና አትላንቲስን ምን አገናኛቸው? ይህን በሌላ ጽሑፍ እመለስበታለሁ።
ዩራነስ የተባለው ፕላኔት የአኳሪየስ ኮከብ መሪ ሲሆን በሥርዓተ ፀሐይ ውስጥ ሰባተኛው የፀሐይ ጭፍራ ነው። ፕላኔቱ ለምዕራባዊያኑ ጠበብት መኖሩ የታወቀው እ.ኤ.አ በ 1781 ቢሆንም በኢትዮጵያውያን ዘንድ ግን ከዚያ ቀድሞ የሚታወቅ ነበር።
የዩራነስ የግኝት ዘመን ከአኳሪየስ ዘመን መቃረብ ጋር የተሰናሰለ ነበር። የርሱን መገኘት ተከትሎ የሳይንስ ዘመን (ኤጅ ኦቭ ሪዝን) ተበስሯል። ዓለም በብዙ ዓይነት አብዮታዊ (ድንገታዊ) ለውጦች ተጥለቅልቃለች።  የፈረንሳይ አብዮትና የሊዮው የናፖሊዮን ጦርነት የዚህ አካል ነበር። በዚህ ጊዜ የመጀመሪያው የኤሌክትሪክ ሳይንስ ሙከራ ተደረገ። የባሪያ ንግድ በህግ ተከለከለ። በዚህ ጉዳይ ዋናው ተዋናይ አኳሪየሱ አብርሃም ሊንከን ነበር። ከዚሁ የዩራነስ ግኝትና ግንነት በኋላ መሀውሮች (ሎኮሞቲቭስ) ተፈጠሩ። አውሮፕላን፣ ቴሌቪዥንና መሰል ፈጠራዎችም ተግተለተሉ። ከዩራነስ ግኝት  እና ግንነት በኋላ በኢትዮጵያ ምን ተስተዋለ? ወዲያው የተፈጠረው ነገር ውዥንብር ነበር። ይኸውም ዘመነ መሳፍንት  እየተባለ የሚታወቀው ጊዜ ነው። ይህ ዘመን ዩራነስ የፈጠረው ድንጋጤና ድንጋሬ ነው።  ሁሉም እየተነሳ እኔ ልንገስ አለ። ነገሩ አስፈላጊ ነበር። በዚሁ ዘመን ኢትዮጵያዊያን ከፍተኛ የሆነ ወደ ኋላ የመቅረት ቁጭት አድሮባቸዋል። ቁጭቱ የዕውቀት ጥማትን ፈጥሯል። በዘመኑ ከነበሩ ነገሥታት ውስጥ የዕውቀት ያለህ እያሉ የጮኹ አስተዋዮች ነበሩበት። ዘመነ መሳፍንት  በዐፄ ቴዎድሮስ መንገሥ ተጠቃለለ። ዐፄ ቴዎድሮስ በጥር ወር መጀመሪያ እንደተወለዱ ስለሚገለፅ ካፕሪኮርን እንበላቸው እንጂ በብዙ ነገረ-ሥራቸው ወደ አኳሪየስነት የተጠጉ መሪ ነበሩ። የሀገር ኮከብ በሦስት መንገድ ይሰየማል። አንዱ ባህሪን በማየት ነው። በዚህ አካሔድ ኢትዮጵያ አኳሪየስ እንደሆነች የፍካሬ ከዋክብት ጠቢባን እየመላለሱ ተናግረዋል። ሁለተኛው መልክዐምድራዊ ነው። በዚህ ልኬት ከነፒቶሎሚ ጀምሮ የኢትዮጵያ አኳሪየሳዊነት የታወቀ ነው። ሦስተኛው የምስረታ ጊዜ ነው። የኢትዮጵያን ቀዳሚ የልደት ቀን አሁን ለጊዜው ማስላቱ አስቸጋሪ ነው። ሌላ ተቀራራቢ ሥነ ዘዴ ግን አለ። ይኸውም የዳግም ልደት ይባላል። በዳግም ልደትም የኢትዮጵያ ኮከብ አኳሪየስ ነው።
የኢትዮጵያ የዳግም ልደት ቀን ዐፄ ቴዎድሮስ  የነገሡበት ዓመት፣ ወር፣ ቀን እና ሰዓት ነው። ይኸውም በአውሮፓውያን አቆጣጠር በ11 ፌብሯሪ 1955 ከጠዋቱ በ3 ሰዓት ከ20 ደቂቃ ላይ (9፡20 AM) በደብረታቦር (11 N 51 38 E 01) ነው። የዚህ ዝርዝር ለሌላ ጊዜ ይቆየን።
ዐፄ ቴዎድሮስ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ጉዳይ ምን ያህል ይቆረቁራቸው እንደነበር ሁላችንም የምናውቀው ነው። ቴዎድሮስ ያለጊዜያቸው የተነሱ መሪ ነበሩ እየተባለ ተደጋግሞ ይነገራል። እርግጥ የተነሱት በመነሻው ዘመን ነው። ችግሩ እሳቸው ተነስተው ህዝቡ ግን አልተነሳም ነበር። ህዝቡ ጋርዶበት ነበር። ይኸ ችግር አሁን ሳይብስበት አልቀረም [አሁንም የጋረደብን ነገር አለ]። ቴዎድሮስ የባርያን ንግድ ተቃውመዋል። ይኸ እንግዲህ ከአብርሃም ሊንከንም የቀደመ ነው። ቴዎድሮስ ሴባስቶፖል የተባለን መድፍም አሠርተው ነበር። ግን አልቀጠልንበትም። አሁን የያዝነው ፈሊጥ አይቻልም ነው። አሁን ስንት ሴባስቶፖል ሠርተን መደነቅ በነበረብን ጊዜ የድሮውን ሴባስቶፖል ብቻ እያመለክን እንገኛለን። ተክለሐዋርያት ከሞስኮብ እንደተመለሱ ዐፄ ምኒልክ ጋ ቀርበው መድፈኝነት እንደተማሩ ነገሯቸው። የንጉሡ ቀዳሚ ጥያቄ “አሁን መድፍን ኢትዮጵያ ውስጥ መስራት እንችላለን?” የሚል ነበር። ከዚያ በኋላ ግን የተጠናወተን አባዜ የመግዛትና በዚያም የመፎከር ነው። ከምንበላው ገምሰን፣ ከሥጋችን ቆርሰን እየሸጥን  አውሮፕላን፣ መኪና፣ ቴሌቪዥን፣ ራዲዮ፣ እርሳስ፣ ወረቀት፣ ኮምፒውተር፣ ሞባይል፣ ወዘተርፈ እንገዛለን።
ቴዎድሮስ ካለጊዜያቸው አልነበረም የተነሱት። በጊዜያቸው ነው። እኛ ግን አልነቃንም። የዓድዋ ድል አኳሪየሳዊት ኢትዮጵያ አይበገሬነቷን ያሳየችበት የአኳሪየስ ዘመን የንጋት ላይ ብስራት ነበር። እኔ የምፈራው ብኩርናችንን በምስር ወጥ እየሸጥን እንዳይሆን ነው። አሁንም ሌላ የዕድል በር እያንኳኳ ነው። የፕሉቶ ፕላኔት ከ2013 ጀምሮ ወደ አኳሪየስ ክምችት ይገባል። ይኸ ሌላው የመነሻ ጊዜ ነው።
ለሚቀጥሉት 30 ዓመታት ከፍ ያለ እመርታ እናስመዘግባለን። ለመጪዎቹ አንድ መቶ ዓመታትም ከዓለም ቁንጮ ሀገራት ቀዳሚ የመሆን ዕድላችን የተጻፈ ነው። እኔ እምፈራው ግን እሱንም ደግሞ ለመሰረዝ ትልቅ ላጲስ እንዳናዘጋጅ ነው።
ኢትዮጵያ ውስጥ መኪና፣ አውሮፕላን፣ ሮኬት፣ የኒኩለር ማበልፀጊያ አይሠራም አትበሉ። ዓለም እኮ ብዙ አልቀደመችንም። ቢበዛ የሀምሳ ወይም የመቶ ዓመት እርምጃ ነው ከፊታችን ያለችው። እድገቷም የጥቂት ግኝቶች ድግግም ነው።
ማጠቃለያ
በእሁድ መዝናኛ ፕሮግራም የታየው የአውሮፕላን ሥራ ሙከራ አስደስቶኛል። ያላሰብኩትን ያናገረኝ እሱ ነው። እመኑኝ እነዚህ ነገሮች ሀሉ ቀላል ናቸው። አይቻልም አትበሉ፤ ይቻላል። እሱማ ሌላስ ጋ ተችሎ የለም እንዴ ? አሁን ማምረቱ ነው እንጂ ይቻላል አይቻልም ማለቱ ሌላ ቁልቁለት መውረድ ይሆናል። ብታምኑም ባታምኑም፣ በሚቀጥሉት 30 ዓመታት ውስጥ ብዙ ትንግርት ያልሆነ ነገር ግን ትንግርት የሚመስል ነገር ይከሰታል። ዕድሜ ከሰጠን እናያለን። የቸኮልኩትም ለዚያ ነው እንጂ መሆኑማ የት ይቀራል!

Published in ህብረተሰብ

ረመዳን በሙስሊም አማኞች ዘንድ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው የተከበረ የፆም ወር ነው፡፡ በረመዳን ሁሉም አማኝ ከምግብ፣ ከመጠጥና ከሌሎች ነገሮች ራሱን አቅቦ መንፈሳዊ አለሙን የሚያንፀባርቅበት ቅዱስ ወር ነው፡፡
ለአምላክ መፀለይ እና በፅኑ መስገድ፣ ለሌሎች ሰዎች መልካም ስነ - ምግባሮችን ማሳየት፣ ምፅዋቶችን መለገስ ከረመዳን መገለጫዎች ውስጥ ጥቂቶቹ ናቸው። በአዘቦት ቀናት የማይሰግዱ ሰዎች እንኳን በረመዳን የአምላክ በረከቶች እንዲያመልጧቸው አይፈልጉም፡፡
የረመዳን ወር ህዝቦች ክፉና በጎውን እንዲለዩ አምላክ መመሪያ ያወረደበት ነው፣ ቁርአንን፡፡ ሰዎች ከአምላካቸው ጋር ያላቸውን ዝምድና እንዲያጠናክሩ ቁርአንን ሲልክ ፈጣሪ የመረጠው የረመዳንን ወር ነው፡፡
እንደ ነብዩ መሐመድ ምክር ከሆነ፣ በረመዳን ፆም ወቅት ሰዎች መጮህ ወይም ለሰደባቸው ሰው መልስ መስጠት የለባቸውም፡፡ ከዚህ ይልቅ “ፆም ይዤያለሁ፤ ፆም ይዤያለሁ” በማለት ከሁከት መራቅ አለባቸው፡፡
የረመዳን ወር ዋንኛ ዓላማ ሰዎች ቀኑን ሙሉ ከምግብ ተከልክለው፣ ስጋቸውን በማዳከም፣ ከአምላክ ጋር ያላቸውን መንፈሳዊ ግንኙነት እንዲያጠናክሩ ነው፡፡ የረመዳን ትሩፋቶችን ተግባራዊ በማድረግ ሰዎች ውስጣዊ ማንነታቸውን መፈተሽ ብቻ ሳይሆን የልቦናቸውን መንፈሳዊነት ማሳደግ አለባቸው፡፡ በፆም ውስጣዊ ተፈጥሯችንን ማዳመጥ ካልቻልን የረመዳን ወር ክብርነት ትርጉሙን ያጣል፡፡ ነብዩም ያስጠነቀቁት ይሄንኑ ነው፡- “ብዙ ሰዎች ከመፆም ምንም ነገር አያተርፉም፤ መራብና መጠማትን ቢሆን እንጂ፡፡” የዘንድሮው የረመዳን ወር እንደጀመረ ሙሐመድ አድ አድናኒ የተባለው የአይሲስ ቃል አቀባይ ከላይ የጠቀስነውን መንፈሳዊነት የሚቃረን አዋጅ ተናገረ፡- “እናንተ ሙጃሒዲኖች ሆይ! በረመዳን ጦርነት በማድረግ ለኢ-አማኞች ወሩን አስቀያሚ አድርጉባቸው፡፡” ይሔው የአይሲስ ቃል - አቀባይ “ማንኛውም አምልኮ ከ(ወታደራዊ) ጂሐድ አይበልጥም” የሚል መግለጫ ከሰጠ በኋላ በረመዳን ሁለተኛው ጁምአ ላይ በኩዌት፣ ቱኒዚያና ፈረንሳይ ውስጥ አሰቃቂ ጥቃቶች ተፈፀሙ፡፡ (የፈረንሳዩን እስከ አሁን ድረስ ኃላፊነቱን ባይወስዱም) ይህ አረመኔ ቡድን፣ በሶሪያ ኮባኒ ውስጥ 145 ንፁሐንን መግደሉን ስንሰማ፣ አይሲስ በቅዱሱ የረመዳን ወር እንኳን የሚራራ ልብ እንደሌለው እንገነዘባለን፡፡ አይሲስ እስልምናን የማይወክል ብቻ ሳይሆን የእስልምናን መለኮታዊ አላማ አፈር ድሜ እያስጋጠ የሚገኝ የጋጠ ወጥ ቡድን ነው፡፡
ፆማችንን የሚመለከተውና የሚፈርደው አንዱ አምላክ ብቻ ነው፡፡ አይሲስ ግን በሳማራ ውስጥ ተደብቃችሁ በልታችኋል ያላቸውን ሁለት ታዳጊዎች፣ እጃቸውን ጠፍሮ አሰቃቂ ግርፋት አድርሶባቸዋል፡፡ በዚህ የረመዳን ወር ሙስሊሞች ሁለ ነገራቸውን ለአምላክ አስገዝተው ባሉበት ወቅት አይሲስ ግን የአማኞች ፀጥታን በማደፍረስ እውነትም የረመዳንን ወር አስቀያሚ አድርጎባቸዋል። አይሲስ እየፈፀመ ባለው ክፉ ተግባር (በረመዳን ወር) የተነሳ ብዙ የእስልምና አዋቂዎችን በቡድኑ እስላማዊነት ላይ ጥርጣሬ እንዲገባቸው አድርጓቸዋል፡፡ አል-ቃኢዳና ታሊባን እንኳን በረመዳን ወር የሚሰነዘሩ ጥቃቶችን ያወግዛሉ፡፡ አይሲስ ግን የረመዳን ፀጥታ መደፍረስ ሳያሳስበው እያደረሰ ያለው እልቂት ብዙዎቹን የእስልምና አለማት ግራ አጋብቷል፡፡ አንድ ነገር ማወቅ ያለብን ከፍጥሪያ በኋላ ያለው የረመዳ ምሽት ለሙስሊሞች የክብረ - በዓል ዓይነት መንፈስ ያለው ነው፡፡ ጎዳናዎች ፆመው በዋሉ አማኞች ይሞላል። ከሽብርተኞች ጋር ግንኙነት አላቸው የሚባሉ ወይም ተባባሪ ሰዎች እንኳን ረመዳን ምሽትን በሰላማዊ መንፈስ ነው የሚያሳልፉት፡፡ አይሲስ ግን በዚህ የረመዳን ወር በሚፆሙ ሙስሊሞች ላይ የጭካኔ ተግባር ፈፅሞባቸዋል። የአይሲስን ተግባር የሚደግፉ አንዳንድ ሰዎች እንኳን በጿሚ ሙስሊሞች ላይ በደረሰው አሳዛኝ ነገር በጣሙን ተቆጭተዋል፡፡
በዲትሮይት ዋይን ስቴት ዩኒቨርስቲ ውስጥ የእስልምና ታሪክ ተመራማሪ የሆነው ሰኢድ ሐሰን በሰነዘረው አስተያየት፡- “በጁምአ ቀን በኩዌት መስጂድ ውስጥ የደረሰው ጥቃት በጣም የሚዘገንን ነው፡፡ በተለይ ደግሞ ምንም ውጊያ ውስጥ የሌሉ ንፁሐን መሆናቸውና በረመዳን  ወር ላይ መፈፀሙ ድርጊቱን የማይታሰብ ያደርገዋል፡፡”
አይሲስ አሁንም እንቆቅልሽ እንደሆነ ነው፡፡ በዋናነት ያነገበው የእስልምናን ሸሪአ በአለም ላይ ማስፈን የሚል አላማ ነው፡፡ ነገር ግን ጥንታዊ የእስልምና ሐገሮችንና ቅርሶችን እያወደመ መሆኑን ስንመለከት “የሸሪአ ህግ ማስፈኑን” ተወው እንዴ የሚያስብል ነው፡፡
በእርግጥ በእስልምና የኋላ ታሪክ ውስጥ በረመዳን ወር ጦርነቶች ተካሂደዋል፡፡ ለምሳሌ በ624 ዓመት የበድር ጦርነት በረመዳን ወር በመነሳቱ ነብዩ ሙሐመድ ይህን ጦርነት መርተዋል፡፡ የጦርነቱ ድል የሙስሊሞች ነበር፡፡ በረመዳን ወር ሌሎች ጦርነቶችም መካሄዳቸው በታሪክ ውስጥ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ ነገር ግን እነዚህ ጦርነቶች የህልውና ጦርነቶች ነበሩ፡፡ ሙስሊሞች በጣኦታውያን ላለመደምሰስ ያደረጉት የሞት-ሽረት ጦርነቶች ናቸው፡፡
አይሲስ ያሳየው ፀብ -ጫሪነትና በሌሎች (ባልታጠቁ ንፁሐን) ላይ የሰነዘረው ጥቃት ግን ከላይ ከጠቀስነው ጦርነቶች በእጅጉ ይለያል፡፡ አይሲስና ተከታዮቹ ስለነብዩ ታሪክና ስለቁርአን ማወቃቸው አጠራጣሪ የሆነውም በዚህ ምክንያት ነው፡፡
አይሲስ እንደሚለው፤ ረመዳን የግድያ ማስፈፀሚያ ወር ነው፡፡ መንፈሳዊ ጥንካሬ፣ ደስታ፣ ለጋስነት እና የአላህ በረከት የተትረፈረፈበት የረመዳን ወር እድሜ ለዚህ አረመኔ ቡድን ክብሩን አጥቷል፡፡ እስልምና ለአእምሯችን እውነታን የምንመግብበት፣ ልቦናችንን በአምልኮ ስርአቶች የምናረካበት ሰላማዊ ሐይማኖት ነው፡፡ የረመዳን ወርን የጭካኔ ማስፈፀሚያ ማድረግ ስህተት ብቻ ሳይሆን የማይታሰብም ጭምር ነው፡፡
ሐይማኖት የእምነት ወይም የስነ-ስርዓት መገለጫ ብቻ አይደለም፡፡ የጠራ ማህበረሰብ መፍጠሪያና እውቀቶችን ከትውልድ ወደ ትውልድ የምናስተላልፍበት ውብ ነገር ነው፡፡ የአንድ ሐይማኖት መንፈሳዊነት፣ ፍልስፍና ወይም እውነታ ከብዙ ሺ ዓመት በፊት ሲወርድ ሲዋረድ ለትውልድ እየተላለፈ የሚመጣ እንጂ ዛሬውኑ የምንፈጥረው አስተምህሮት አይደለም፡፡ በሐይማኖት ውስጥ የዚህ ዓይነት ልማዶችን መገንዘብ አማኞች ምን ማድረግ እንዳለባቸው ማንም አይነግራቸውም፤ ራሳቸው ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡ ወይም ደግሞ ይህን ለምን ፈፀምኩት? ለሚሉት ጥያቄዎች መልስ ማግኘት አያቅታቸውም፡፡
የአይሲስን አካሄድ በደንብ ካጤነው ግን ለትውልድ እየተላለፈ ከመጣው ትሩፋት ጋር ምንም ግንኙነት እንደሌለው እንረዳለን፡፡ የኋላ ትሩፋቶችን ከእውነት ጋር አጥብቆ ያልያዘ ትውልድ ደግሞ እጣ-ፈንታው መጥፋት ብቻ ነው፡፡ መሰረት የሌለው ግንብ ማለት ነው፡፡ እኛ ግን አሁንም ቢሆን ይህ ግንብ እስኪፈርስ ድረስ ደመ-ከልብ ለሆኑትና ለሚሆኑት ንፁሐን ሰዎች ከልብ ማዘናችንንና ፀሎት ማድረሳችንን አናቆምም፡፡  

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 04 July 2015 10:34

የኪነት ጥግ

(ስለ ፋሽን)
- ጎበዝ የሆነች ሞዴል ፋሽንን በ10 ዓመት
ልትቀድመው ትችላለች፡፡
ይቭስ ሴይንት ሎውሬንት
- እኔ ፋሽን አልሰራም፡፡ ራሴ ፋሽን ነኝ፡፡
ኮኮ ቻኔል
- ልብሶችን ዲዛይን አላደርግም፡፡ እኔ ዲዛይን
የማደርገው ህልሞችን ነው፡፡
ራልፍ ሎረን
- ፋሽን ያልፋል፤ ስታይል (ሞድ) ዘለዓለማዊ
ነው፡፡
ይቭስ ሴይንት ሎውሬንት
- ሴቶች የሚፈልጉትን አውቃለሁ፡፡ የእነሱ
ፍላጎት መዋብ ነው፡፡
ቫሌንቲኖ ጋራቫኒ
- ሽቶ የማትቀባ ሴት ተስፋ የላትም፡፡
ኮኮ ቻኔል
- ስታይል ሳትናገሩ ማንነታችሁን
የምትገልፁበት መንገድ ነው፡፡
ራሄል ዞ
- አንድ ሰው አይተኬ ለመሆን ምንጊዜም
ከሌላው መለየት ይኖርበታል፡፡
ኮኮ ቻኔል
- አለባበስ የኑሮ ዘይቤ ነው፡፡
ይቭስ ሴይንት ሎውሬንት
- እያንዳንዱ ትውልድ በድሮ ፋሽን ይስቃል፤
አዲሱን ግን የሙጥኝ ብሎ ይከተለዋል፡፡
ሔነሪ ዲቪድ ቶሬዩ
- የፋሽን ዲዛይነር ብሆንም ሻንጣዬን በብዙ
ቁሳቁሶች አልሞላም፡፡
ሪም አክራ
- ልብሶችን በማጥለቅና በወጉ በመልበስ
መካከል ልዩነት አለ፡፡
ዋየኔ ክሪሳ
- ግሩም ልብስ ከጥሩ ጫማ ጋር ያምራል፡፡
ሁለቱን መነጠል አትችልም፡፡
ዋይኔ ክሪሳ
- ምንም እንኳን የወንዶች ዓለም ቢሆንም
ሴት መሆኔን እወደዋለሁ፡፡ ወንዶች ቀሚስ
መልበስ አይችሉም፤ እኛ ግን ሱሪ መልበስ
እንችላለን፡፡
ዊትኒ ሂዩስተን
- ለልጃገረድ ተስማሚውን ጫማ ስጧት፤
ዓለምን ድል ትነሳለች፡፡
ማርሊን ሞንሮ
- የማስበው በጥቁር … ነው፡፡
ጋሬዝ ፑግ

Published in ጥበብ
Saturday, 04 July 2015 10:30

የፀሐፍት ጥግ

ኑርሁሴን
ሂሮዬ ሺማቡኩሮ
(ስለ ሃያስያን)
- ለማንም ሙገሳም ሆነ ወቀሳ ትኩረት አልሰጥም።
እኔ የምከተለው ስሜቴን ብቻ ነው፡፡
ዎልፍጋንግ አማዴዩስ ሞዛርት
- መፃፍ የሚችሉ ይፅፋሉ፤ መፃፍ የማይችሉ
ይተቻሉ፡፡
ማክስ ሃውቶርን
- አብዛኞቻችን ዘንድ ያለው ችግር በትችት ከመዳን
ይልቅ በሙገሳ መጥፋትን መምረጣችን ነው፡፡
ኖርማን ቪንሰንት ፒል
- ወጣቶች ሞዴሎችን እንጂ ሃያስያንን
አይፈልጉም፡፡
ጆን ውድን
- ሂስ የሚጠይቁ ሰዎች የሚፈልጉት ውዳሴ ብቻ
ነው፡፡
ሶመርሴት ሟም
- ልብህ ትክክል መስሎ የተሰማውን አድርግ፡፡
ትችት እንደሆነ አይቀርልህም፡፡
ኢልኖር ሩስቬልት
- አንድ ሰው ሌሎችን ለማውገዝ ከማሰቡ በፊት
ራሱን ለረዥም ጊዜ መመርመር አለበት፡፡
ሞሌር
- ሃያሲ ስንዝር ከሰጠኸው ተውኔት ልፃፍ ይላል፡፡
ጆን ስቴይንቤክ
- ሂስ የተወለደው ከኪነጥበብ ማህፀን ውስጥ
ነው፡፡
ቻርልስ ባውድሌይር
- ጠንካራ አስተያየቶች የሚሰነዘሩት በሚወዱህ
ሰዎች ብቻ ነው፡፡
ፌዴሪኮ ማዮር
- ሃያሲያን በሥነ ፅሁፍና በሥነ ጥበብ ዘርፍ
ያልተሳካላቸው ሰዎች ናቸው፡፡
ቤንጃሚን ዲስራኤሊ
- አንበሳም ቢሆን ራሱን ከዝንቦች መከላከል
አለበት፡፡
የጀርመናውያን አባባል
- የጎረቤትህን ቤት ብታቃጥል ያንተን ቤት የተሻለ
ገፅታ አያጎናፅፈውም፡፡
ሎ ሆልትዝ
- ሃያስያን ለሚናገሩት ትኩረት አትስጥ፡፡ ለሃያሲ
ክብር ፈፅሞ ሃውልት ቆሞለት አያውቅም፡፡
ዣን ሲቤሊዩስ

Published in ህብረተሰብ

     ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ የመጣሁት ከ13 ዓመት በፊት ነበር - በሙያ መምህርነት ለማገልገል። ተማሪዎቹ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲያዩኝ ጃፓናዊ መሆኔ ትኩረታቸውን ሳይስበው አልቀረም፡፡ በዚህም የተነሳ ስለራሴና ስለጃፓን የማይጠይቁኝ ነገር አልነበረም። የሚገርማችሁ ያን ጊዜ በቦሌ መንገድ ላይ እንኳን ብዙ የውጭ ዜጐች አይታዩም ነበር፡፡ የኢንተርኔት አገልግሎትና ሳተላይት ቲቪ አልነበረም፡፡ እናም ብዙ ጊዜዬን የማሳልፈው ለተማሪዎቼ ስለ ጃፓን በማውራት ነበር፡፡  
በኋላማ የጃፓን ባህልን የማስተምርበት ክፍለ ጊዜ (Cultural class) ሁሉ ጀምሬ ነበር - ስለጃፓን የበለጠ ለማወቅ ጉጉት ያላቸውን ሰዎች ፍላጐት ለማርካት፡፡ ምክንያቱ ባይገባኝም  ተማሪዎቼ ብቻ ሳይሆኑ ሌሎችም ሰዎች እኔን ከሌላ ፕላኔት እንደመጣሁ አድርገው የመመልከት አዝማምያ ይስተዋልባቸው ነበር፡፡ ብዙዎቹ የምለውን ነገር ለመስማት ከፍተኛ ጉጉት ነበራቸው፡፡ አንዳንዴ በማደርጋቸው ነገሮችም ጭምር ይገረሙ ነበር። ምናልባት ከኢትዮጵያ ባህልና ወግ የተለየ ሆኖባቸው ሊሆን ይችላል፡፡   
ያን ጊዜ በአዲስ አበባ አብዛኛው ሰው የመስመር ስልክ ተጠቃሚ ሲሆን ሞባይል ስልክ እንደብርቅ ነበር የሚታየው፡፡ ሰዎች በህዝብ ስልክ ለመደወል ወረፋ መያዝ ይጠበቅባቸው ነበር፡፡ ያኔ መዲናዋም እንዲህ በትራፊክ አልተጨናነቀችም፡፡ ረዣዥም ህንፃዎችም በጣት የሚቆጠሩ ነበሩ፡፡
ሁሌ ትዝ የሚለኝ ፈረንጅ ጓደኞቼ በሳምንቱ የእረፍት ቀናት (ቅዳሜና እሁድ) የምንዝናናበት አጣን እያሉ ያማርሩ እንደነበር ነው፡፡ ለነገሩ እውነታቸውን ነበር፡፡ ያን ጊዜ እቃ ለመሸመት እንኳን የሚጐበኙ ትላልቅና ዘመናዊ የገበያ አዳራሾች የሉም ነበር፡፡ የሚያወላዱ የመዝናኛ ሥፍራዎችም አልነበሩም! የአሁኖቹ እነ ደምበል፣ ፍሬንድሺፕ፣ ኤድናሞል… መች ነበሩ! (ኤድናሞል የተሰራበት ሥፍራ ባዶ ሜዳ ነበር)
ያኔ…አዳዲስ የወጡ የሆሊውድ ፊልሞችን መመልከቻ ሲኒማ ቤት አልነበረም፡፡ አምባሳደር ደግሞ ምናልባት የህንድ ፊልሞችን ቢያሳይ ነው፡፡ እንደነ ቦስተን ያሉ ደረጃቸውን የጠበቁ የውበት ሳሎኖች፣ ሳውናዎችና ማሳጅ ቤቶችም አልነበሩም … እነዚያ ፈረንጅ ጓደኞቼ ታዲያ ፀጉራችንን የት እንሰራ? የት ማሳጅና ሳውና እናድርግ? ምናምን እያሉ ሲነጫነጩ ትዝ ይለኛል፡፡
ያኔ ካልዲስንና ቤሉስን የመሳሰሉ ምርጥና ዘመናዊ ካፌዎችን አስሶ ማግኘት ዘበት ነበር፡፡  ብዙዎቹ ደረጃቸው ዝቅ ያለ ተራ ካፌዎች ሲሆኑ በአብዛኛው የድለላ ሰራተኞችና ጎልማሶች አንድ ስኒ ቡና ይዘው ለሰዓታት የሚቀመጡባቸው ቦታዎች ነበሩ፡፡ በዚህ የተነሳ ማኪያቶ እየጠጡ ዘና ማለት እንኳን መከራ ነው በተለይ ለፈረንጅ ጓደኞቼ፡፡
ለእኔ ግን ሁኔታው ፈጽሞ የተለየ ነበር፡፡ ባይገርማችሁ… የሳምንቱ የዕረፍት ቀናት ለእኔ አስደሳችና አዝናኝ ነበሩ፡፡ ለምን መሰላችሁ? ኢትዮጵያውያን ጓደኞቼ ቤት ተጋብዤ ስለምሄድ፣ ከወዳጅ ዘመዶቻቸውና ጎረቤቶቻቸው ጋር ምሳ እንበላና ቡና ተፈልቶ እየጠጣን እናወጋለን፡፡ ቡናው ሲያከትምም በወቅቱ የነበረውን ብቸኛ የቲቪ ቻናል (ኢቲቪን) ለረዥም ሰዓት አብረን እንመለከታለን፡፡ አንዳንዶቹ የቲቪ ፕሮግራሞች አሰልቺ ቢሆኑም ዝም ብለን እናያቸው ነበር፡፡ በእውነቱ ያ ጊዜ ለእኔ ልዩ ትዝታን ጥሎብኝ አልፏል፡፡
ከ13 ዓመት በፊት ጃፓንን ከመሰለ የሰለጠነ ዓለም ለመጣ ሰው፣ አዲስ አበባ በጊዜ ሃዲድ የኋሊት ተንሻትታ የጥንት ዘመን ላይ የቆመች ነበር የምትመስለው፡፡ መዲናዋ ከብዙ ነገሮች አንፃር የድሮ ጊዜ ላይ ነበረች ማለት ይቻላል። ለእኔ ግን ግሩም ትውስታዎችን በውስጤ ማስቀረት የቻልኩበት ወቅት ነበር፡፡ ቡና እየጠጡ ማውጋት… ከኢትዮጵያውያን ቤተሰቦች ጋር መብራት ጠፍቶ በጨለማ የበቆሎ ጥብስ መብላት፣ መንገድ ላይ የወደቀ ሰው ለመርዳት መረባረብ የመጐራረስና እንብላ የማለት ባህል፣ እርስበርስ ለመረዳዳት መትጋት …ይሄ ቀላል ግን በጃፓን እምብዛም የማይገኝ የበለፀገ የማህበራዊ ህይወት ተሞክሮ ነው፡፡
በአገሬ ጃፓን ሰዎች ስለሌላው ሰው ብዙም ደንታ የላቸውም፡፡ የሰዎች ግንኙነትም ቢሆን ግልብ ነው። ሁሉም በግል ህይወቱ ምሕዋር ነው የሚሽከረከረው።  በዚህ የተነሳ በአዲስ አበባ ያስተዋልኩት ድንቅ የመተሳሰብና የመደጋገፍ ባህል እንዲሁም ግሩም ማህበራዊ ህይወት በውስጤ ታትሞ ቀርቷል፡፡
ይሄ ሁሉ ከ13 ዓመት በፊት የነበረ ታሪክ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ነገሮች እንዴት በፍጥነት እንደተለወጡ ለእናንተ አልነገራችሁም፡፡ አዲስ አበባ በእጅጉ ተጨናንቃለች - በሰውና በተሽከርካሪ፡፡ በእርግጥ ሰዎች  በኮንዶሚኒየም ቤቶች ውስጥ መኖር ጀምረዋል፡፡ የ24 ሰዓት አገልግሎት የሚሰጡ በርገር ቤቶችና ማሳጅ ቤቶች በየቦታው ተከፍተዋል፡፡
አሁን የሞባይል ስልክ ለአዲስ አበቤ ብርቁ አይደለም፡፡ በህዝብ ስልክ ለመደወል ወረፋ መያዝም ቀርቷል፡፡ የቤት ሰራተኛና ጥበቃ ሳይቀሩ የሞባይል ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን እንደ ድሮው አንድ ቻናል ሳይሆን በርከት ብሏል፡፡ በዚያ ላይ የሳተላይት ቲቪ እንደልብ ሆኗል፡፡ እናም ሰዎች የምዕራብ አገራትን ፊልሞች እያማረጡ ይኮመኩማሉ፡፡ ምን ይሄ ብቻ… የኮርያና የቱርክ ተከታታይ የቲቪ ድራማዎችን ከሳተላይት የቲቪ ቻናሎች ላይ አድነው የሚመለከቱ ወጣቶች አሉ፡፡
ከሁሉም በላይ ደግሞ የኢንተርኔት መስፋፋት በሰዎች ህይወት ላይ ጉልህ ለውጥ አምጥቷል፡፡ ኢትዮጵያውያን ለመረጃ ቅርብ ሆነዋል፡፡ በፌስቡክ አማካኝነት ከጃፓናውያን ጋር ጓደኝነት የመሰረቱ ጥቂት አይደሉም፡፡ አሁን ሰዎች ስለጃፓን ማወቅ የሚፈልጉት ነገር ቢኖር እንደድሮው እኔን መጠየቅ አያስፈልጋቸውም። ከ Wikipedia ላይ ያሻቸውን መረጃ ያለ ስስት የማግኘት ዕድል ተፈጥሮላቸዋል፡፡
ከ13 ዓመት በፊት ሴቶች ለብቻቸው እንኳንስ ባርና የምሽት ክለቦችን ሊያዘወትሩ ቀርቶ ካፌና ሬስቶራንት የሚገቡትም ከስንት አንድ ነበሩ፡፡ በተለይ በምሽት ሴት መጠጥ ቤት ከታየች ሌላ ስም ይሰጣት ነበር፡፡ ይሄ ግን አሁን ተለውጧል፡፡ ዛሬ ኢትዮጵያውያን ሴቶች የወንድ አጃቢ ሳያስከትሉ ወደ ምሽት ክለቦች ጎራ ብለው ሲዝናኑና ሲደንሱ ማየት እንግዳ ነገር አይደለም፡፡  በአብዛኛው የፈረንጆች መናኸሪያ የነበሩት እንደነሸራተን ያሉ ውድ ሆቴሎች አሁን በኢትዮጵያውያን ደንበኞች መሞላት ጀምረዋል፡፡
ዛሬ ኢትዮጵያውያን የቢዝነስ ሰዎች በእጅጉ በስራ ከመጠመዳቸው የተነሳ ሰው ሲቀጥሩ እንደ ድሮው በደፈናው “ነገ ብቅ በይ” ማለት ትተዋል፡፡ የምትመጡበትን እቅጯን ሰዓት ካልተናገራችሁ እሺ ብለው ቀጠሮ አይሰጧችሁም፡፡ አሁን የቢዝነስ ሰዎች የጊዜ  ጥቅም እየገባቸው መጥቷል፡፡  
በአዲስ አበባ ባለፉት 13 ዓመታት የተለወጡትን ነገሮች ዘርዝሬ የምጨርሰው አይመስለኝም፡፡ ከፈጣኑ ለውጥ ጋር በርካታ ነገሮች አብረው  መጥተዋል፡፡ ሰዎች ከመቼውም ጊዜ የበለጠ በርካታ መረጃዎች ማግኘት ችለዋል፡፡ ብዙ የሚሰሩ ቢዝነሶች… ብዙ የሚገዙ ነገሮች ብዙ የሚጐበኙ ቦታዎች …ብዙ ማህበራዊ ግዴታዎች… ብዙ ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች… ተፈጥረዋል፡፡ በዚህም የተነሳ አዲስ አበቤ ቀን ተሌት ባተሌ ሆኗል፡፡ ማታ ተሰባስቦ ቡና የሚጠጣበት ሰዓት እንኳን እየጠፋ ነው፡፡
በነገራችን ላይ የአዲስ አበባ ሱፐር ማርኬቶች እንደ አገሬ ጃፓን ጣጣውን የጨረሰ የቡና ዱቄት (Instant Coffee) ማቅረብ ሁሉ ጀምረዋል፡፡ ያ የምወደው ባህላዊ የቡና አፈላል ሥርዓት ቀስ እያለ እንዳይጠፋ እሰጋለሁ። ለነገሩ አሁንም ጐረቤት ቡና መጠራራት በእጅጉ ቀንሷል። እንደምዕራብ አገራት ከጐናቸው ያለውን ነዋሪ (ጐረቤት) ማንነት የማያውቁ አዲስ አበቤዎች በርክተዋል፡፡ ህይወት ሩጫ ሆናለች፡፡ መሮጥ …መሮጥ… መሮጥ… ትልቅ ትንሹ ባተሌ ሆኗል፡፡
ወላጆች እንዲህ በኑሮና በሥራ ተወጥረው ሲዋከቡ ህፃናትን የሚያስታውሳቸው ይጠፋል፡፡ ብዙ ህፃናት በሞባይል ጌም ወይም በቲቪ ጌም ተጠምደው ነው የሚውሉት፡፡ ሌሎቹ ደግሞ ወደ ቲቪ ላይ አሊያም የአኒሜሽን ፊልሞች ላይ አፍጥጠው ይውላሉ፡፡ እኒህ ጥሩ ምልክቶች አይመስሉኝም፡፡ የኢትዮጵያውያን የዳበረ ማህበራዊ አኗኗርና የመረዳዳት በጐ ባህል ፈጽሞ በዕድገትና ሥልጣኔ መደፍጠጥ የለበትም፡፡ በተገኘችው ጊዜ ሁሉ ቡና ተሰባስቦ መጠጣትና ማውጋት፣ የተቸገረን መርዳት፣ ልጆች ታላላቆቻቸውን እንዲያከብሩ ማስተማር አስፈላጊ ነው፡፡
ዘመናዊነት የማይተካቸው እሴቶች እንዳሉ ማወቅ ብልህነት ነው፡፡ ለዕድገት ስትተጉ ባህላችሁንም አትዘንጉ!!


Published in ህብረተሰብ