በወግ ፀሐፊነቱ የሚታወቀው በኃይሉ ገ/እግዚአብሔር የጻፋቸው በማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ መጣጥፎች የተካተቱበት “ኑሮ እና ፖለቲካ- ቁ 3” የተሰኘ አዲስ መፅሃፍ ትትሞ ለንባብ ቀረበ፡፡ መፅሃፉ ቀላል የማይባሉ አዳዲስ ሥራዎች እንደተካተቱበት የጠቆመው ደራሲው፤ ቀድሞ የተሰሙና የተደመጡትም እንኳ በደጋሚ እንዲነበቡ ተደርገው በደንብ መቃናታቸውንና አዳዲስ ነገር እንደተጨመረባቸው ለአዲስ አድማስ አስታውቋል፡፡ በ157 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ለአገር ውስጥ በ40.50፣ለውጭ አገር በ15 ዶላር ይሸጣል፡፡  ደራሲው ከዚህ ቀደም “መንታ መልኮች”፣ “ኑሮ እና ፖለቲካ” (ቁጥር 1 እና 2) የሚሉ መጻህፍትን ያሳተመ ሲሆን በተለያዩ የፕሬስ ውጤቶች ላይ በአሽሙር የተጠቀለሉ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ወጎችን በማቅረብም ይታወቃል፡፡

“ቦቃፍ ቡሬ” የተሰኘ አዲስ የኦሮምኛ ኮሜዲ ፊልም፣ የኪነጥበብ ባለሙያዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ባለፈው ሳምንት ሐምሌ 12፣ በኦሮምያ የባህል ማዕከል በተከናወነ ደማቅ ስነ-ስርዓት የተመረቀ ሲሆን በሲዲ ለሽያጭ እንደቀረበም ታውቋል፡፡
በታምራት አዳሙ ተጽፎ በታዴማ ሚዲያ ኤንድ ኢቨንት ኦርጋናይዘር ኤክስኪዩቲቭ ፕሮዲዩሰርነት እና በኢሉ ኮ ፕሮዳክሽን ተሰርቶ የቀረበውን #ቦቃፍ ቡሬ#፣ ዳይሬክት ያደረገው ራሱ ታምራት ሲሆን የአንድ ሰዓት ከ30 ደቂቃ ርዝማኔ አለው፡፡ሰርቶ ለማጠናቀቅ 7 ወር በፈጀው በዚህ ፊልም ላይ አንጋፋው ተዋናይ አድማሱ ብርሃኑና ኦሊ ነጋ በመሪ ተዋናይነት የተጫወቱበት ሲሆን ሌሎች ከ15 በላይ አንጋፋና ወጣት ተዋንያንም ተሳትፈውበታል ተብሏል፡፡

ቀጠሮዬ “ይብሳ ህንፃ” ነው፡፡ ህንፃው በያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤትና በጃንሜዳ መካከል እንደሚገኝ ተነግሮኛል፡፡ በቅጡ ስለማላውቀው እየጠየኩ ወደዚያው አዘገምኩ፡፡ ከያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት አንፃር ሲታይ አካባቢው ላይ ሁለት ባለ አራት ድርብ ህንፃዎች ብቻ አሉ፡፡ አንዱ ተጠናቋል፣ ሌላኛው በመገንባት ላይ ይገኛል፡፡ “የትኛው ይሆን?” እያልኩ ጥቂት እንደተጓዝኩ መንገደኛ ጠየኩ፡፡ “ይብሳ ህንፃን” አሳዩኝ፡፡
 መጀመሪያ አላመንኩም፡፡ መልሼ ሌላ ሰው ጠየቅሁ፡፡ በድጋሚ ያንኑ ቤት አመላከቱኝ፡፡
ግር አለኝ …
… “ይብሳ ህንፃ” በሸክላ የተሰራ መደዳ ቤት ነው፡፡ ደርብ የሚባል የለውም፡፡ ታዲያ ስለምን “ህንፃ” ተባለ? ማንም ሊነግረኝ አልቻለም፡፡ ሁሉም የሚያውቀው “ይብሳ ህንፃ” መባሉን እንጂ ለምን እንደተባለ አይደለም፡፡ ከመመርመር ወደ መጠርጠር ተሸጋገርኩ፡፡ በአፄ ምኒልክ ዘመን አካባቢው ላይ “ከላሾች” ሰፍረው ነበር፡፡ “ከላሾች” ቀላህ ሰብስበው እርሳስ እያቀለጡ አረር በመሙላት ለዳግም ጥይትነት የሚያበቁ ሙያተኞች ናቸው፡፡ በወቅቱ ከላሾቹ የጥይቱን ሜዳ ላይ ደርድረውና በጣሳ ሰፍረው ይሸጡ እንደነበር ታሪክ ይነግረናል፡፡ እነዚህ ከላሾች ጥይት አረር የሚሞሉበት ሥራቸው ሆዳቸውን ሞልተው ከማደር ውጪ ጥሪት ለመሰብሰብ የሚያስችል አልነበረምና የሚኖሩበት ጎጆም እንደ ነገሩ የተጠጋገነ ነበር፡፡ እንግዲህ ከእነሱ መካከል ፊውራሪ ይብሳ አንድ ቀይ ሸክላ ቤት አስገነቡ፡፡ ለአካባቢው ብርቅ እና ድንቅ ከመሆኑም ባሻገር ከሩቅ የሚታይ መለያም ጭምር ነበር፡፡ ስለዚህ ቤቱ በንፅፅር ደምቆ በመታየቱ የገዘፈ ሥም አገኘ “ይብሳ ህንፃ”፡፡
ሳቅኩ!! በዕድሜ ጠገቡ ቤት ላይ ሳቅኩ፡፡ እኔ አይደለሁም የሳቅኩት ትውልድ ነው፡፡ አባቶች ካሉበት ዘመን አንፃር ነፅረው ያገዘፉት ለእኔ ኮሰሰብኝ፡፡ መጀመሪያ “ይብሳ ህንፃ” ስባል ለግምት እዝነ ልቦናዬ ላይ የተደረደሩት የዘመኑ ህንፃዎች በታሪኬ ላይ እንድስቅ አስገደዱኝ፡፡ ትውልድ እንዲያ ነው፡፡ ተቀባብሎ የማደግ ሰዋዊ የተፈጥሮ ህግ ከትንሽ ወደ ትልቅ መጓዝን ግድ ይላል፡፡ ባለፈው መሳቅ ከማገናዘብ በፊት ይቀድማል፡፡ ትውልድ እንዲሁ ነው፡፡
በመጀመሪያው ካሜራ ቢሳቅ የትውልድ ወግ ነው፡፡ የሚከራይ ቤት መስሎን ስንጠይቅ ካሜራ መሆኑ ሲነገረን ለምን አንስቅ? እንስቃለን!! ጡሩንባ መስሎን ያየነው፣ የመጀመሪያው ግራማፎን መሆኑ ሲነገረን አሁንም እንስቃለን!! ምክንያቱም ትውልድ አሻሽሎ የሰጠን ለማንፀሪያነት አለን፡፡
… የሚያሳዝነው ግን የትውልድ “ሳቁ” በሁሉም ዘርፍ አይተገበርም፡፡ በተለይ የእኛን አገር ሙዚቃ፣ ሥዕል፣ ስፖርት፣ ሥነ-ፅሁፍ … ስንቃኝ ትውልድ በቀደመው ትውልድ ከመደመም ወጥቶ ለሳቅ አይዳዳውም፡፡ ጥላሁን ገሠሠና ዘመኑ የዚህ ትውልድ መሰረት ሳይሆኑ ከላያችን ያሉ ጣሪያዎች ናቸው፡፡ ለምን? የአገኘሁ እንግዳ ሥዕሎች እንደ “ይብሳ ህንፃ” የሚሳቅባቸው እርቀት ላይ አይደለንም፡፡ ለምን? እግር ኳስ እነመንግሥቱ ወርቁ ጋ ቀርቷል ብለን ስለምናስብ የዘመኑን ጨዋታ በእነ ሳልሀዲን ሳይሆን በእነሱ ብንገጥም እንደምናሸንፍ ደምድመናል፡፡ ለምን? በአማርኛ ሥነ-ፅሁፍ ውስጥ ጥቂት ደራሲያን ብቻ የመጀመሪያም የመጨረሻም ተደርገው ተደምድሟል፡፡ የመጀመሪያ መባላቸው ይሁን፤ እንዴት የመጨረሻ ተብሎ በእነሱ ተደመደመ? ለምን? ….
… ተፈጥሯዊውን የትውልድ ዕድገት መርህ ተፃርረን!! የኋሊት ብቻ የመመልከት ዕጣ - ለእራሳችን አውጥተናል፡፡ የትውልድ አቅጣጫ ወደፊት መሆኑን ዘንግተናል፡፡ በአዲስ ጎዳና ላይ ያለፈ ትውልድ ዱካ እንፈልጋለን፡፡ ያንን ዱካ ለመሳፈር እንቃብዛለን፡፡ ኦታምፑልቶ (ኢትዮጵያዊው ደራሲ በቅርቡ በ Penguin Book የታተመለት አንድ መፅሐፍ አለ፡፡ ርዕሱ “Catch your Thunder” ይሰኛል፡፡ እዚህ 517 ገፅ ያለው ሥራ ውስጥ ትውልድን ከእግር ዱካ ጋር አጣምሮ የሚመረምር ንዑስ ምዕራፍ አለ፡፡ “The root prints that you see ahead of you are not that of your ancestors. They rather are of your children.” እውነት ነው፤ ያለፈ ትወልድ ዱካ እንዴት መጪ ትውልድ መንገድ ላይ ይነጠፋል? ምንጊዜም ከፊትህ የሚገኘው ፈለግ የልጅህ እንጂ የአባቶችን ሊሆን አይችልም፡፡
… ይብሳ ህንፃ መለስ ብለን የምናየው የአባቶቻችን እግር ፈለግ ነው፡፡ ከዘመኑ ውጪ ሲታይ ስያሜው ይከብደዋል፤ ህንፃ መባሉ ያዋርደዋል፡፡ ይህ እንዲህ የሆነው በግንባታ መለስተኛ የትውልድ ቅብብል ስለተከናወነ ነው፡፡ ፍርቅርቁ አሁን ለንፅፅር የሚታዩ ጥቂት ህንፃዎች ዘንድ አድርሶናልና፡፡ እስክናገናዝብ የፌዝ ሳቅ ቢያመልጠን ለታሪክ ፍርድ አንቆምም፡፡ በተፃራሪው በሙዚቃ፣ በሥዕል፣ በስፖርት፣ በሥነ ፅሁፍ… የትውልድ ቅብብል ስላልተከናወነ ይሆን ባለፉት ስራዎች የፌዝ ሳቅ የማያመልጠን? የግማሽ ምዕት ትውልድ ምን ዋጠው? ዱካውን ምን ሰለበው? ምንስ ሲሰራ መሽቶ ነጋለት? እንዴትስ ከሱ በፊት የነበሩትን መጋረድ ተሳነው? … እነዚህ ጥያቄዎች የሚቀርቡ የተለያዩ ምላሾች አሉ፡፡ አንደኛው የነቢይ መኮንን ተሃዝቦ ነው፡፡ “ሥውር ስፌት ቁ.1” ላይ “ደረጃ የሌለው መሠላል” በተሰኘ ርዕስ እንዲህ ይላል፡-
ይሄ ያገሬ ሰው እኮ፣ መሠላል አወጣጥ ያቃል
አንዱን እርከን ረግጦ ሲያልፍ፣ ነቅሎ ጉያው
ይከተዋል
ደሞ ቀጣዩን ይረግጣል …
ነቅሎ ጉያው ይከተዋል …
እንዲህ እንዲያ እያለ ዘልቆ፣ ከዝና በላይ
ይወጣል፤
ከጥቅምም በላይ ይሰፍራል …
እንደኮራ እንደተዝናና፣ ቃል ሳይናዘዝ ይሞታል፡፡
በቀብሩም ሥርዓት ላይ
“ደግ ለሰው አሳቢ
ለተቸገረ ደራሽ…”
የሚል የህይወት ታሪክ ወግ፣ ይፋ ይነበብለታል። ከቀን በኋላም ገኖ፣ ሀውልቱ ገዝፎ ይታያል፡፡
ያም የደረጃ እርከን - እንጨት፣ መቃብር አጥሩ ይሆናል!!
የትውልድ መንገድ አግዳሚ የሌለው መሰላል መሆኑ መወጣጫ ነሳን፡፡ ስለዚህ ያለፉትን አንጋጦ መመልከት የህይወት ፍልስፍናችን ሆነ፡፡ ታሪክ እንደ ትልም፣ ነባር እንደ ግብ ታየ፡፡ እንደ መስታወት ክትር ከጀርባችን የምንደብቀው፣ የምንጋርደው አጣን፡፡ እንደሌለን ሆንን፡፡ አባቶቻችን በእኛ ላይ የምንግዜም አንደኛ ሆኑ፡፡ ልጆችን በእኛ ዘንድ የምንጊዜም ምንም ሆኑ፡፡ የትውልድ ንብብሮሽ ፈረሰ፡፡ አንዱ ከሌላው ማጅራት አልፎ ማየት ተሳነው፡፡ ቅብብሎሹ ተዛነፈ፤ ሰጪ ተቀባይ፣ ተቀባይም ሰጪ አጣ …
… ትውልድ ሲቀበል ልደቱ ሲሰጥ ሞቱ ይከናወናል፡፡ እኛ ዘንድ ልደትም ሞትም የለም፡፡ ትወልድ አልጌ ተከናንቦ ረግቷል፡፡ የሚያፋስሰው አጥቷል፡፡ የሚያነባብረው የሙሴ በትር ተነስቷል፡፡ እይታችንን ዳፍንት፣ ቁመታችንን  ክፋት አሳጥሮብናል፡፡ የታየን እንደግማለን፣ በተደረሰበት ቁመታችንን እንለካለን …
… እንግሊዛዊው ሳይንቲስት አይዛክ ኒውተን (1642-1727) ስለትውልድ ንብብሮሽ የሚለው አለው፡፡ “If I have seen a little farther than others, it is because I have stood on the shoulders of giants.” (በጥቂቱም ቢሆን ከሌሎች በተሻለ አርቄ ለመመልከት የቻልኩበት ምክንያት በግዙፉ ትከሻ ላይ በመቀመጤ ነው፡፡)
አዲስ ትውልድ በጥቂቱም ቢሆን አሻግሮ መማተር ካልቻለ፣ የነባሮቹ ትውልድ ትከሻ የለም ማለት ነው፡፡ ትውልድ የመደዳ ድርድር ከሆነ የሚታየው ከማጅራት ፈቅ አይልም፡፡ ደራሲ አዳም ረታ “በአዲስ ነገር” ጋዜጣ ላይ ያለው ይሄንኑ ነው ያለው፡፡ “ያለፉት ትውልዶች ትከሻ እንደጠርሙስ ልሙጥ ነው፤ አያስቀምጥም” እንደ ይብሳ ህንፃ በሀዲስ አለማየሁ፣ በበዓሉ ግርማ፣ በፀጋዬ ገብረመድህን፣ በመንግሥቱ ለማ … ላይ መሣቅ ያቃተን ለዚህ ነው፡፡ ከማጅራት ከፍ ባላለ እይታ በምንና በማን አንፅረን በሥነ ፅሁፎቹ “ይብሳ ህንፃዎች” ላይ እንሳቅ???

Published in ጥበብ

 በመስከረም አበራ የተፃፉ የተለያዩ ፖለቲካዊ መጣጥፎችን ያካትተው “ስለ ስልጣን” የተሰኘ አዲስ መፅሃፍ ሰሞኑን ታትሞ ለንባብ ቀረበ፡፡ መፅሃፉ በ7 ምዕራፎች የተከፋፈለ ሲሆን  “የብሄር ፖለቲካችን”፣ “የአቶ መለስ ትዝታዎች”፣ “ቅይጥ ፖለቲካዊ ጉዳዮች” እና ሌሎችም ርዕሶችን አካትቷል፡፡
በ230 ገፆች የተቀነበበው “ስለ ስልጣን”፤ በ57 ብር ከ65 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡
ፀሃፊዋ በተለያዩ የፕሬስ ውጤቶች ላይ ፖለቲካዊ መጣጥፎችን በማቅረብ ትታወቃለች፡፡

Monday, 27 July 2015 11:15

የኪነጥበብ ጥግ

(ስለ ኮሜዲ)
እኔ ጣቴን ስቆርጥ ትራጄዲ ነው፡፡ አንተ ክፍት ቱቦ ውስጥ ገብተህ ስትሞት ኮሜዲ ነው፡፡
ሜል ብሩክስ
ህይወት፡- ለብልሆች… ህልም፣
       ለሞኞች… ጨዋታ፣
       ለሃብታሞች … ኮሜዲ፣
       ለድሆች … ትራጀዲ ነው፡፡
                    ሻሎም አሌይቼም
የኮሜዲ ሥራ ሰዎችን እያዝናኑ ከጥፋታቸው ማረም ነው፡፡
ሞሌር
ኮሜዲበ ሌሎች ሰዎች ላይ የሚከሰት ትራጄዲ ነው፡፡
አንጄላ ካርተር
ሳቅንና ስቃይን፣ ኮሜዲንና ትራጄዲን፣ ጨዋታንና ጉዳትን የሚለይ ቀጭን መስመር አለ፡፡
ኢርማ ቦምቤክ
ህይወት በቅርት ሲታይ ትራጀዲ፣ በርቀት ሲታይ ኮሜዲ ነው፡፡
ቻርሊ ቻፕሊን
የኮሜዲ ትርኢት ላይ የምትመጡት ለመዝናናት ነው፡፡
ቢል ኮስቢ
የራስን ዝምታ ማዳመጥ የኮሜዲ ቁልፍ ነው።
ኢላይኔ ቡስለር
ኮሜዲ ለሰው ልጅ ብቸኛ ተስፋ ነው፡፡
ሮዝአኔ ባር
ነፃ ትግል ለእኔ እንደ ስታንድ አፕ ኮሜዲ ነበር፡፡
ዲዋይኔ ጆንሰን
እውነተኛ ኮሜዲ ሰዎች እንዲስቁና እንዲያስቡ ብቻ ሳይሆን እንዲስቁና እንዲለወጡም ያደርጋል፡፡
ሳም ኪኒሶን
ኮሜዲ የሚመነጨው ከውዥንብር ነው፡፡
ቪር ዳስ
ኮሌጅ በመሄድ ፋንታ ኮሜዲ መስራትን መረጥኩ፡፡
ቦ ቡርንሃም

Published in የግጥም ጥግ
Monday, 27 July 2015 11:13

የሣሮን ዝምታ

  እነዚያ በክዋክብት መሀል የተሞሸሩ የሚመስሉ ዓይኖችዋ መኝታዬ ድረስ መጥተው ሲንቦገቦጉ፣አልጋዬን አልፈው ልቤ ለብቻዋ አገላብጠው ሲጠብሷት መነሳት ግድ አለኝ፡፡ ነፍሴ ብቻዋን እስክስታ እየመታች፣ በሳቅዋ ደወል ትዝታ ስትሰክር ውሎ ማደር ለምዶባታል፡፡ ግን በጧት ከባድ ነው፡፡ ገና ጀንበር ቅንድብዋን ሳትገልጥ፣ ገና አድማሳት በብርሃን ፌሽታ ቀሚስ ሳይቀይሩ …
ብድግ አልኩና ከወይራ ሰፈር ኮንዶሚኒየም ግቢ ወጣሁ፡፡ ደግነቱ ታክሲ አለመጥፋቱ፡፡ ከግራና ከቀኝ “ጦር ኃይሎች … ጦር ኃይሎች” እያሉ ዘፈኑን ጀመሩት፡፡ ብፈልግ አውጉስታ ጫፍ ድረስ---ካሰኘኝም ቀጠና ሁለት ሙሉ ወንጌል ድረስ እሳፈራለሁ፡፡ የወይራ ሰፈር ክፋቱ ኩላሊት እሰኪታመም ድረስ ታጭቆ መሄድ ነው፡፡ ዋናው ሰልፍ ይዞ አለመገተር ነው አልኩ በልቤ፡፡ በተለይ እንዲህ ናፍቆት ባሳደደ ቀን … ህይወት ለንቦጭዋን በጣለች ጊዜ፡፡
ትርጉም የለሽ ናት ህይወት፡- ልል ነበር፡፡ … ግን አንዱ ትርጉምዋ ይሄ አይደል! … በፍቅር ዓይኖች ጥቅሻ እየነፈሩ ወደ ቀጣዩ ምዕራፍ መንጎድ! … ተውኩትና አሰብኩ፡፡ ያበሳጨኝ የሳሮን ናፍቆ ብቻ አይደለም፡፡ አይኖችዋ የልቤን እርቃን በብርሃን ልምጭ ስለዠለጡትም አይመስለኝም፡፡ … እነዚያን የውበትና የፍስሀ ኃይላት መቆጣጠር ባለመቻሌ ነው፡፡ ስድስት ወር ሙሉ አብሬያት ስንገላወድ ኖሬ ፍቅረኛ ያለማድረጌ! አልጫ ነገር ነኝ! …
ቀጠና ሁለት ደረስኩና ቴዲ ካፌ ገባሁ፡፡ መስከረም የቡናው ማሽን ላይ ቆሟል፡፡ በድሩ ፈጥኖ  መጣና ታዘዘኝ፤ ወይም አየኝ፡፡ ጠቀስኩት፡፡ ከማኪያቶ ሌላ ጠጥቼ አላውቅም፡፡
ብርጭቆዋ እስክትሰክር ድረስ አጣፍጦ ሰራልኝ፡፡ እያጣጣምኩ አወረድኳት፡፡ አሁን ግን በጧት መውጣቴ ምን እንደሚረባኝ አላወኩም፡፡ ሽሽት መሆኑ ነው፡፡ ብቻዬን አልጋ ላይ ስታገኘኝ እንዳትዘነጣጥለኝ ፈራሁ፡፡ ልቤን---አንጀቴን---ኩላሊቴን----ጉበቴን…. ከራስ ፀጉር እስከ እግር ጥፍሬ! …
 በካፌው የግድግዳ መስታወት ውጭው ወለል ብሎ ይታያል፡፡ ታክሲዎች ተደርድረዋል፡፡ ቀራንዮና የሺ ደበሌ ይጠራሉ፡፡ ከፊሉ ደግሞ ከወይራ ሰፈር መጥተው ቆመዋል፡፡ ሰው ይተራመሳል፡፡ ከታች ከቻይና ኤምባሲ በኩል የሚመጣው፣ እንደገና ወደ ታች የሚወርደው ብዙ ነው፡፡
“እ…. እንዴት ነበር? ማኪያቶው?”  አለኝ መስከረም! የአውራ ጣቴን ቀስሬ አሳየሁት፡፡ ቀሽት ነው ማለቴ ነው፡፡ ማመስገን ነበረብኝ… አንዳንዴ ደንበኛ ደስ ሲለው፣ ደስ እንዲላቸው ምላሽ ይፈልጋሉ፡፡ ቲፕ እንኳ ቢቀር የአንደበት ምስጋና!
ሞባይሌን አውጥቼ ልደውልላት አሰብኩ፡፡ ግን ደግሞ በዚህ ጠዋት ምን ብዬ ነው የምደውልላት! … ስድስት ወር ሙሉ ሳንቀላፋ ቆይቼ ዛሬ በዛሬ ምን ልፈጥር ነው? … የዛሬ አራት ዓመት የኮሌጅ ጓደኛዬ ያለችኝ ትዝ ይለኛል፡፡ “… እንዴ መቼ ነው ከእንቅልፍህ የምትባንነው! ኧረ ንቃ!” ብላኝ ነበር፡፡ ለዚያውም ከተለያየን በኋላ ያንን ያህል ስታወራኝ፣ ያን ያህል  ጉያዬ ውስጥ ስትገባ፣ ጡት እንደምትጠባ ወላድ ዝም ብዬ ማለፌ የገባኝ ቆይቶ ነው፡፡ አሁን ሳሮንስ እንደዚያ ሆና ከሆነ ለማንኛውም ይለይላታል፡፡
ለነገሩ አሁን ብደውል እንኳ ምናልባት ሥራ ላይ ልትሆን ትችላለች፡፡ የሬዲዮ ስቱዲዮ ቴክኒሻን ናት፡፡ የእነርሱ ሥራ አንዳንዴ በምሽትም ሊሆን ይችላል፡፡ ማለዳም እንደ ወፍ ከሚንጫጫው ጋዜጠኛ ጋር አጅባ ትንጫጫ ይሆናል፡፡ የአዳም ፍጡር፣ ጧት ማታ እንጀራ! ጧት ማታ ኑሮ! … ወደ ፍልስፍናው መሄድ አስቤ፣ ፍልስፍና ትንሽ ችኮ ነው፡፡ ፍቅር ለስላሳ ነው፡፡ ፍቅር አበባ ቢሆን፣ ፍልስፍና እሾህ ነው፡፡ በጧት ደ‘ሞ እሾህ ምን አመጣው?
ሚስቴ ብትሆን ግን ያስጠላኝ ነበር፡፡ ከሞቀ መኝታችን ውስጥ ምዝዝ ብላ ጥላኝ ስትሄድ አንጀቴ ይቃጠላል፡፡ በተለይ በክረምት! … ለነገሩ ሲጀመርስ አገባታለሁ ብዬ መች አሰብኩ፡፡ ድንገት ስለ አርክቴክቸር ላወራ ሬዲዮ ጣቢያ ተጋብዤ ስተነትን አይደል አይን ለአይን የተጋጨነው፡፡ ከዚያ በኋላ ከስቱዲዮ ስወጣ ጨብጣኝ፤“ንግግርህ ያምራል!” እነዚያ ኳስ አይኖቿ ናቸው እየተከተሉ እንደ ርችት ሲፈነዱብኝ የከረሙት፡፡
ያን ያህል ግን ማራኪ ንግግር ነበረኝ እንዴ? … ያወራሁት ስለ ኪነ-ህንፃ የየዘመኑ መልክነትና የጀርባ ትርጓሜ ነበር፡፡ ምናልባት ስለ አውድም አውርቼ ይሆናል፡፡ በርግጥም ከታላላቅ ሰዎች ሀሳብ ጋር አጣጥሜ ትንሽ ውበት ነስንሼለት ነበር፡፡ … ግን ለቅን ልቦና … በርዋን ለከፈተች ነፍስ ያ በቂ ነው፡፡ ልብዋ በር ላይ ውሻ አስራ ቢሆን አስደንግጦኝ ነበር፡፡ የልብዋ በር ግን የአበባ እርሻ ነው፡፡ ያስታውቃል፡፡
ማልታ “… ሃይ ድጋፌ!” አለኝ ድንገት፡፡
ቀና ብዬ አየሁት፡፡ የፊት ጥርሶቹ የሉም፡፡ ባርኔጣውን እያስተካከለ - ተቀመጠ፡፡
“ሰማህ ዛሬ አርሰናል!”
ሊጨቀጭቀኝ ነው፡፡ ዝም አልኩት፡፡
“ድሮ መንግስቱ ወርቁ! … ፓ!... ለጊዮርጊስ ሲጫወቱ!”
ፈረደብኝ፡፡
“በል ልጋብዝህ ቡና ጠጣ!”
“እዚህ ቤት ማልታ የለም!..”
“በቃ ቡና ጠጣ!”
ከንፈሩን አጣመመ፡፡
“እኔ የራሴ ኳስ ሜዳ ውስጥ ነኝ” ልለው ፈልጌ ተውኩት፡፡
ማልታ ደስ ሳይለው ቡና አዝዞ አጠገቤ ተቀመጠ፡፡ ብቻዬን መሆን ፈልጌ ነበር፡፡ ይሉኝታ አልያዘኝም፡፡ የሁለታችንንም ከፍዬ ቁልቁል ወደ ቸኮላት ካፌ ወረድኩ፡፡ እዚያ ሰገነት ላይ ወጥቼ ቁልቁል እያየሁ፣ቢያሻኝ ማንጎራጎር ባይሆን ስልክ ደውዬ እንደ ልቤ ማውራት እችላለሁ፡፡ ማኪያቶ መድገም አልፈለግሁም፡፡ በቅመም ያበደ ሻይ አምጪልኝ አልኳት፡፡ ፈገግተኛ አስተናጋጅ ናት፡፡
እዚያ አሰብኩ፤ ቴአትር ልጋብዛት ይሆን? መቸም እሷ ከቴአትር ይልቅ ፊልም እንደምትመርጥ አውቃለሁ፡፡ እኔ ግን ፊልም ማየት አይመቸኝም፡፡ አእምሮ እንዳስለመዱት ነው፡፡ ጎመንም ሆነ ጮማ እንደ ሰውየው ነው፡፡ ታክሲ ይዤ ወደ ሜክሲኮ ብሄድ የመገናኘት ዕድልም ይኖረን ነበር፡፡ ግን ደ‘ሞ የጦር ኃይሎችን የታክሲ ፍልሚያ ማን ይችለዋል! … ማርፈድ አለብኝ፡፡
 ብቻ ክብ ቀይ ፊትዋ፣ ጥርሶችዋና ድምፅዋ እየመጡ ይረብሹኛል፡፡ ሰሞኑን የፌስ ቡክ አካውንት የከፈትኩትም፣ እስዋ እየከፈተች ስታቀረቅር አይቼ ነው፡፡ ፍቅር ያጃጅላል’ኮ… #ታዲያ ፌስቡክ ውስጥ ለምን አልፈልጋትም፡፡ ደግሞስ ፕሮፋይሏን ለምን አላነበውም፡- ጥሩ ዘዴ መጣልኝ; አልኩና አጎነበስኩ፡፡ ከፈትኩት፡፡
ፌስቡክ ብዙ ደስ አይለኝም፡፡ ጓደኞቹ ሲያወሩኝና ሲያሳዩኝ ብዙ ነገሩ ግልብ ነው፡፡ ውስጧ የማይታወቅ የሴት ሥዕል እያዩ ማጨብጨብ አይደል እንዴ! … ድንቅ ነው! … ልዩ ነሽ! ማለት፡፡ ውስጧ ሲታይ ደግሞ ገለባ ሆነ ትገኛለች፡፡ በዚያ ውብ መልኳ የተገረመን ወንድ እንደገና እንደ እንስሳ እርቃን በማሳየት ፍየልነቷን ታስመሰክራለች፡፡ ወንዱስ ቢሆን? ጢሙን አንዠርግጎ አንበሳ በመሰለ ፊቱ፣ የህፃን ልጅ ቀልድ ሲቀልድ ወይም ወደ ተወለደበት ቀንና ሥዕል ሲወርድ ይደብራል፡፡
የሳሮንን ከፍቼ አየሁት፡፡ ብዙ ሳሮኖች አሉ፡፡ ጥቁር፣ ጠይም፣ የቀይ ዳማ፡፡ ፀጉረ ዞማ፣ ፀጉረ ቁርንድድ! … አቤት የሄዋን ዘሮች! ወዲያው የሄድኩት ወደ ራሴ ሳሮን ነው፡፡ ፎቶግራፏን ተራ በተራ ፈተሽኩ፡፡ ሰውነቴ ሳላውቀው በላብ ተነከረ፡፡
“ከስንት ወንዶች ጋር ነው ተቃቅፋ የተነሳቸው?… ከሦስት?” አጭበርባሪ ናት ለካ! ነደደኝ፡፡ ቆይ ፍቅረኛ አለኝ ማለት አትችልም እንዴ? … ይህን ያህል ስንግባባ! … ወይስ “ንፁህ ወንድሜ ነህ! … በሚል ሽንገላ ልትጠፈንገኝ! እንደዚያ የፍቅር እሳት የሚተፉ አይኖችዋ  በአይኖቼ በኩል ገብተው ልቤን ሲያርሱት አታውቅም? … ባላየው ይሻለኝ ነበር ይሆን? … ማየቴ ክፋት የለውም፡፡ ግን ለምን እንዳልነገረችኝ መጠየቅ አለብኝ፡፡
“ሻዩ አልተመቸህም?” አለችኝ አስተናጋጅዋ፡፡ ፊቷ ተለዋውጧል ማለት ነው፡፡
“አይ ደህና ነው!” አልኳትና ለሰው ስለሚጨነቁ ሰዎች አሰብኩ፡፡ ይህቺ አስተናጋጅ ባለችበት ሁኔታ ሰው እንዲያዝን አትፈልግም ማለት ነው---ብዬ የሳሮንን ሀጢያት ልጨምር ሞከርኩ፡፡ “ምናልባት የአጎትዋ ልጆች… የአክስቷ ልጆች ቢሆኑስ?” እንደገና ላየው ሞከርኩ፡፡ የአጎት ልጅ እንደዚህ ወገብ ጨምድዶ ፎቶ አይነሳም፡፡ ትከሻዋ ላይ እጁን ቢጥል ነው፡፡
ቁጥሯን መታሁ፡፡ በሳቅ ጀመረች፡፡ ዘንቦ እስኪያባራ ጠበቅሁ፡፡ የሰማይ ሙዚቃ ነው፡፡ ምትሀት አለው፡፡
“ምነው በሰላም”
“ፌስቡክሽን ከፍቼ አየሁት!”
ፀጥ አለች፡፡
“ምን አየህ?”
“ሁሉንም ነገር በተለይ ፎቶግራፎችሽ!”
“ፎቶግራፎቹን እቀይራቸዋለሁ ብዬ ነበር፣ ታሪኬን የሚያውቁ ሰዎች ከለከሉኝ;
“እንዴት?”
“አንዱ የዛሬ ዓመት ገደማ ያረገው ጓደኛዬ ነው፡፡”
“ወዴት ወደ ሰማይ?”
“አ…ዎ!”
“አልገባህም! … ቦይ ፍሬንዴ ነበረ! …”
“እ….ና?”
“ አ-ረ-ገ!”
“ምን ማለት ነው፡፡
“ከዚህ ዓለም ተለየ!”
“ታዲያ ሞተ አትይኝም!”
“ተ-ው! .. ተው!... እንደሱ አይባልም!”
“ከሌላው ሰው ይለያል እንዴ አሟሟቱ?”
“ተው ስለሞት አታውራ!”
“ምነው ሳሮን አዲስ አይደለም’ኮ!”
“ለኔ አዲስ ነው፡፡ … ከእርሱ ቀድመው ሦስት ቦይ ፍሬንዶቼ አርገዋል”
“ሞተዋል ማለት ነው?”
“አንተ በለው … እኔ ግን ዳግም እንዳይደርስብኝ - ይህን ቃል አትጠቀሚ ተብያለሁ፡፡ … ስለምፈራ ነው፡፡ ፎቶግራፋቸውን እንዳላወጣ ደ‘ሞ ቤተሰቦቻቸው ያዝናሉ!; አማተብኩ፡፡ የት አባቴ ልደበቃት? … እኔም የተንቀዠቀዥኩት ከእነርሱ ጋር ለማረግ ነው? ከኪሴ ውስጥ ሂሳቡን እንዴት አድርጌ እንዳወጣሁት አላውቅም፡፡ ጠረጴዛ ላይ ወርውሬ ሸሸሁ፡፡ “ቆይ መልስ አለህ!” የሚለው የአስተናጋጅዋ ድምፅ ተከትሎኛል፡፡ እኔቴ ዞር ብዬም አላየሁ፡፡ … የልቤ ምት ግን ይሰማኛል፡፡

Published in ልብ-ወለድ
Monday, 27 July 2015 11:12

ግብር እና ክብር

  ልብ የሚሰውረው ማሳሰቢያ ለመጀመሪያ ጊዜ የደረሰኝ፤ ገና ‹‹ተደላድዬ ልኖር ነው›› ባልኩበት ወቅት ፤ትርጉሙን በቅጡ ባልተረዳሁት ስያሜ ራሱን ‹‹ገማች›› ነኝ ብሎ ባስተዋወቀኝ በአንድ እንግዳ ሰው በኩል ነበር፡፡ ከዚህ ቀደም እሱ የተሰማራበትን አይነት የሙያ ዘርፍ ሰምቼ እንደማላውቅ ነገርኩት፡፡ ቢሆንም በመገናኘታችን ተደስቻለሁ፡፡ እናስ አረፍ ይል ይሆን? አዎ ተቀመጠ፡፡ ቀጥዬ ምን ብዬ ወሬ እንደምጀምር የማውቀው ነገር አልነበረም፡፡ ያው መቸም ሰዎች በህይወት ውስጥ ትልቅ ስፍራ በሚሰጠውና እንዲህ እኔ  ዛሬ እንደደረስኩበት ባለ በራሳቸው የመኖሪያ ቤት ውስጥ የመኖር ደረጃ ላይ ሲደርሱ፣ በማህበረሰቡ ውስጥ ተግባቢ፤እንግዳ ተቀባይና ሰው ወዳጅ መሆን ይጠበቅባቸዋል የሚል ስሜት አደረብኝ፡፡ ያም ሆኖ የቻልኩትን ያህል ባስብም ምንም የምለው ነገር ስላጣሁ፤ ምናልባት በዚህ ሰፈር ውስጥ ሱቅ የከፈተ ጎረቤታችን ይሆን እንደሁ ጠየቅሁት፡፡
ምላሹ አዎን ነበር፡፡ (ምንም የማላውቅ ሰው ሆኜ መታየቱን በፍፁም አልፈቀድኩም ፤ ይልቅስ በሱቁ ውስጥ ምን ምን እንደሚሸጥ እንዲያወራልኝ ፈለግሁ)
በደፈናው ‹‹እሺ ታዲያ ንግድ እንዴት ነው?›› ብዬ ስጠይቀው፤ ‹‹ደህና ነው›› ብሎ መለሰልኝ፡፡
ከዚያም ቀጠልኩና ሱቁን እንደምንጎበኝለት፣ ከሌሎች የተሻለ ሆኖ ካገኘነውም ቋሚ ደንበኞቹ እንደምንሆነው ነገርኩት፡፡
እርሱም በተራው፤የሥራ ቦታውን መውደዳችን እንደማይቀር እንደሚያስብና ሌሎች ስፍራዎችን የሚያስንቅ ብቃት ያለው መሆኑን፣ አንድ ጊዜ የእሱ አገልግሎት ተጠቃሚ ከሆነ በኋላ በተመሳሳይ ተግባር የተሰማራ የእሱ አይነት ሰው ፍለጋ ለመሄድ እግሩን ያነሳ አንድም ደንበኛ አጋጥሞት እንደማያውቅም ነገረኝ፡፡
አነጋገሩ በራስ መተማመን ይንፀባረቅበት ነበር፡፡ ምንም እንኳን ባብዛኞቻችን ላይ የሚስተዋልብን ራስን በብቃት መግለፅ ያለመቻል ተፈጥሯዊ ድክመት ቢታይበትም፤ ሰውየው ሁኔታው ሁሉ እምነት የሚጥሉበት አይነት  ነበር፡፡
እንዴት እንደ ጀመርነው ባላውቀውም ብቻ ቀስ በቀስ በጣም የመቀራረብ ሁናቴ ይታይብን ጀመር፡፡ እናም ንግግሮቻችንም የቅርብ ወዳጅነት መንፈስ ፈጠሩና ቆይታችን የምር ላፍታም የማይጎረብጥ ምቹ ጊዜ ሆኖ ነበር ያለፈው፡፡
በቃ አወራን አወራን አወራን - ቢያንስ ይህን ከማድረግ አልቦዘንኩም፡፡ እናም ሳቅን ሳቅን ሳቅን - እርሱም ቢያንስ ይህን ማድረግ ችሎ ነበር፡፡ ቢሆንም ግን በቆይታችን ጊዜ ሁሉ በጣም ጥንቁቅ ነበርኩ ፤ ከአስተዳደጌ ያካበትኩትን ‹‹በሰው ፊት ሙሉ ሆኖ የመታየት››ን ጥበብ ተጠቅሜ፡፡ የእንግዳውን ሰው ምጥን እና ቆጠብ ያሉ ምላሾቹን እየገነገንኩ፤የንግዱንና የገቢውን ምስጢር ሁሉ አብጠርጥሬ ለማወቅ ቆርጬ ነበር፡፡ ስለ ስውር ወጥመዴ አንዳችም ጥርጣሬ ሳይገባው ገመናውን አውጥቶ እንዲዘረግፍልኝ ለማድረግ ተዘጋጀሁ፡፡ በቃ በጣም ጥልቅና ረቂቅ የሆነ ሴራ ጎነጎንኩለት ማለት ይቻላል፡፡ በመጀመሪያ እኔ ስለ ራሴ የገቢ ምንጮች ዘርዝሬ እነግረዋለሁ፡፡ ያኔ በየዋህ መሳይ ተፈጥሮዬ በጣም ይመሰጥና ጥንቃቄውን ይዘነጋዋል፡፡ ከዚያም፤በቅን የጓደኝነት መንፈስ በምንቆይበት በዚያች እኔ ምን እያደረግሁ እንዳለሁ ባላወቀባት ፋታ፣ ቁጥብነቱን ወዲያ ትቶ ዘና ይልና የግል ገቢውን ምስጢር ሁሉ ይዘከዝክልኛል ማለት ነው፡፡ እናም ‹‹ጌታው፤ በአሁኑ ሰአት እያወራህ ያለኸው እንዴት ካለ ድንቅ ሰው ጋር እንደሆነ ብዙም የምታውቀው ነገር የለም!›› ልለው አሰብኩ፤ ያልኩት ግን ሌላ ነበር…
‹‹ለተሰበሰቡ ሰዎች በማቀርበው የዲስኩረኝነት ስራዬ ብቻ ምን ያህል ገቢ እንዳገኘሁ ብነግርህ በፍፁም ማመን አትችልም!››
‹‹አዎን፤ አልችልም ብል ነው የሚሻለኝ፤በኋላ ገምቼ ከማፍር ማለቴ ነው፡፡ ግን እንደው ዝም ብዬ ለመገመት እንድሞክር ከፈቀድክልኝ… ወደ ሁለት ሺህ ዶላር ገደማ ምናልባት…አይ! አይሆንም! ምክንያቱም ጌታው፤መቸም ያን ያህል ገቢ ልታገኝ እንደማትችል አውቃለሁ፡፡ እሺ አንድ ሺህ ሰባት መቶ ይደርስ ይሆናል ልበል?››
‹‹ሀ!ሀ!ሀ! ልትገምት አትችልም ብዬህ ነበር’ኮ፡፡ ባለፈው የፀደይ ወርና በዚህ ክረምት ለዲስኩሬ ብቻ የተከፈለኝ አስራ ሰባት ሺህ ሰባት መቶ ዶላር ነው! እሺ ምን ተሰማህ ?››
‹‹ኦው! ይኸ በጣም የሚደንቅ ነው! በእውነት በጣም ይገርማል! በማስታወሻዬ ላይ መያዝ አለብኝ፡፡ እናም ደግሞ ይኼም ቢሆን ሁሉም ገቢዬ አይደለም እያልከኝ ነው?››
‹‹ሁሉም?! ትቀልዳለህ እንዴ የተከበርከው ወዳጄ? በዛ ላይ ከጋዜጣ ጽሁፎቼ የማገኘው ክፍያዬ አለ! ከ ዴይሊ ዋርሁፕ ጋዜጣ ወደ…ወደ…አዎ! ለምሳሌ፤ እሺ እንደው ምን ትል ይሆን...በአራት ወራት ጊዜ ውስጥ ወደ ስምንት ሺህ ዶላር አካባቢ አግኝቻለሁ ብልህስ?››
‹‹ኸረ በል! ማን ይከለክልሀል የፈለግከውን ብትልስ? እኔስ ብሆን እንዲህ ባለው የገቢ ውቅያኖስ ውስጥ መዋኘትን እመኛለሁ ከማለት በቀር ሌላ ምን ሊወጣኝ ይችላል ብለህ? ስምንት ሺህ፡፡ ይኼንንም በማስታወሻዬ ላይ አሰፍረዋለሁ፡፡ ወቸ ጉድ! እንዳልከውም እንዴት ያለኸው ድንቅ ሰው ኖረሀል እባክህን! እኔ እምልህ፤ አሁንም ከነዚህ ኹሉ በላይ ሌላም ተጨማሪ ገቢ እንዳለህ ገና ልትነግረኝ እንደምትችል መጠበቅ ይኖርብኝ ይሆን?››
‹‹ ሀ!ሀ!ሀ! ምን ሆነሀል? እና? ገና ጫፍ ጫፉን ብቻ’ኮ ነው የሰማኸው፡፡ መጽሐፍ ጽፌ ነበር - ‹‹ንጹኃኑ ግዞተኞች›› የሚል - ዋጋው ከሦስት ከሀምሳ እስከ አምስት ዶላር ነው - እንደ ተዳጎሰበት የጥራዝ አይነት ይለያያል፡፡ እንግዲህ በደንብ አድምጠኝ…አይን አይኔን እያየህ፤ባለፈው አራት ወራት ከአስራ አምስት ቀን ውስጥ፤ከዚያ በፊት ምንም አልተሸጠም ማለት ይቻላል፤ባለፈው አራት ወር ከግማሽ ግን ዘጠና አምስት ሺህ መጻሕፍትን ሸጥን፡፡ ዘጠና አምስት ሺህ ኮፒ! አስበው እስቲ…ዋጋውን ስታጠጋጋው በአማካይ አንዱ መጽሐፍ በአራት ብር ሂሳብ እንደ ማለትኮ ነው፡፡ እና? ምታዋ!...አራት መቶ ሺህ ዶላር አካባቢ አይመጣም የተከበርከው ወዳጄ? ከዚያ ውስጥ ግማሹ የኔ ድርሻ ሆነ እልሀለው!››
‹‹የፈጣሪ ያለህ! ይኼንንም እመዘግበዋለሁ! አስራ አራት፣ሰባት፣ ሃምሳ፣ስምንት፣ ሁለት መቶ… በድምሩ ወደ…አዎ…ወደ… ይኸን ለማመን ይከብደኛል! ድምሩ ወደ ኹለት መቶ አስራ ሶስት ወይም አስራ አራት ሺህ ዶላር! ትክክል ነኝ?››
‹‹ትክክል! ስህተት ቢኖር እንኳን ከአደማመር ችግር የመጣ ነው የሚሆነው፡፡ እንጂ ብዙ ነው፡፡ ብቻ ምናለፋህ የዚህ አመት አጠቃላይ ገቢዬ እቅጩን ሁለት መቶ አስራ አራት ሺህ ዶላር ነው፡፡ ሊያውም ባግባቡ አሳክቼ አስልቼው እንደሁ እንጃዪ…!››
ከዚያም ሰውየው ለመሄድ ከተቀመጠበት ብድግ አለ፡፡ ጭራሹኑ ለማላውቀው መጤ ሚስጥሬን ሁሉ በከንቱ መዘክዝኬ ውስጤን ይጎረብጠው ጀመር፡፡ ገና ለገና እንግዳው በታላቅ መደነቅ ስለጮኸልኝ ብቻ ገቢዬን ጨማምሬ ያለመጠን እያጋነንኩ በመንገር ላሳምነው ሁሉ ጥረት አድርጌያለሁ፡፡ እንደፈራሁትም በኋላ ጉዳዩ ሌላ ሆነና ተገኘአ! የተከበረው እንግዳዬ፤ልክ ሲሰናበተኝ የታሸገ ትልቅ ፖስታ እጄ ላይ አኖረልኝና፤በእሽጉ ውስጥ እስካሁን የመዘገባቸውን ማስታወሻዎች ጨምሮ የእርሱ ሙያ ምን እንደሆነም በቂ ግንዛቤ ከሚያስጨብጠኝ መረጃ ጋር በዝርዝር እንደማገኝ እናም እንደኔ አይነት የገቢ ምንጭ እንዲኖረው ያለውን ምኞት አንፀባርቆ፤ ቢያንስ ግን እንደኔ ካለ የትየለሌ ገቢ በሚያስገኙ የስራ ዘርፎች ከተሰማራ ሰው ጋር የሥራ ግንኙነት በመፍጠሩ ከፍተኛ ኩራት እንደተሰማው፤ በከተማው ውስጥ የሚኖሩና ሀብታሞች ናቸው ብሎ የሚገምታቸው በርካታ ሰዎች መኖራቸውን፤ ሆኖም  ከእነርሱ ጋር በሚያደርገው ይህን መሰሉ የሥራ ግንኙነት ቆይታው ጊዜ ግን ኑሯቸውን በመከራ የሚገፉ ምስኪኖች ሆነው እንደሚያገኛቸው፤ ከዚህ አንፃርም በእውነቱ በጣም ከረዥም ጊዜ በኋላ ገና ዛሬ እንደኔ ያለ ታማኝ ሀብታም ፊት ለፊት አግኝቶ ክብር ተሰጥቶት፣ማውራቱና እጄን በእጆቹ  መንካቱም እንዳስገረመው ገልፆልኝ፤ ስሜቱን መቆጣጠር በተሳነው አይነት ክንዶቹን ዘርግቶ ሊያቅፈኝ ቃጣና የግዱን ተወት ሲያደርገው አስተዋልኩ፡፡ በርግጥም የፈለገውን እንዲያደርግ ብፈቅድለት እንደ ትልቅ ውለታ እንደሚቆጥረው ከአኳኋኑ ያስታውቅ ነበር፡፡
ሁኔታው አንጀቴን ስለበላኝ ልከለክለው አቅም አነሰኝና፣እንስፍስፉ እንግዳዬ እጆቹን በአንገቴ ዙሪያ ጠምጥሞ ጥቂት የእንባ ዘለላዎችን በትከሻዬ ላይ እንዲያንጠባጥብ ፈቀድኩለት፡፡ ከዚያም ወጥቶ ሄደ፡፡
ገና እግሩ ከበር እንዳለፈ የሰጠኝን እሽግ ከፈትኩት፡፡ በውስጡ ያገኘኋቸውን ወረቀቶችም ለአራት ደቂቃዎች ያህል በትኩረት አጤንኳቸው፡፡ ወዲያውም ምግብ አብሳዬን ጠራሁና ምን አልኩ …
‹‹ራሴን ስቼ ስወድቅ ደግፈኝ››
ከጥቂት ሸለብታ በኋላ ስነቃ፤ከህንፃው በታች ካለው የመንገዱ ጥግ ሰው ልኬ አንድ ጠንቋይ አስጠራሁና ሥራ ቀጠርኩት - ሌሊቱን ሙሉ ቁጭ ብሎ ያንን እንግዳ ሰውዬ እንዲረግምልኝ!
ወይ ጉድ! ምን ያለው እርጉም ሰው ነበር! በፖስታው ውስጥ የነበረው የድግስ ጥሪ ካርድ አልነበረም፤ የአመት ገቢዬን ማረጋገጫ ሰነድ ነበር- በገቢዬ ልክ ግብር እንድከፍል የሚሞሉ ቅጾች፤ስለ ግል ህይወቴም አላስፈላጊና ዝርዝር መረጃዎችን እንድሰጥ የሚያባብሉ፣በጥቃቅኑ የተፃፉ መደዴ ጥያቄዎች ከታጨቁበት አራት ገፆች ጋር፡፡ “እነዚህ እንኳንስ እኔና ምናልባትም በዓለም ላይ የፈለገ ያህል እውቀት ያካበተ ዕድሜ ጠገብ አዛውንትም ቢሆን ሊረዳቸው የማይችላቸው ጥያቄዎች ናቸው!# ብዬ ምላሽ ከመስጠት የሚያግደኝ ያለ አይመስለኝም፡፡ መጠይቆቹ፤ገና ለገና እያንዳንዱ ሰው ሳይዘላብድ ትክክለኛውን የአመት ገቢውን እንዲያምን ለማድረግ ሲባል በቅፆቹ ላይ ገቢውን በአራት እጥፍ አባዝቶ እንዲሞላ የተቀናበሩ አይነቶች ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ ከዚህ ከተዘፈቅኩበት ማጥ የማመልጥበትን መንገድ ማሰላሰል ያዝኩ፡፡ ግን አንድም መሹለኪያ ቀዳዳ አልታይህ አለኝ፡፡ ጥያቄ ቁጥር 1 ብቻውን ጉዳዩን ሁሉ ጠቅልሎ አይኔ ስር ሰተረልኝ…
ባሳለፍነው የበጀት አመት አጠቃላይ ገቢዎ ምን ያህል ነበር? ከማንኛውም የንግድ ልውውጦች? ከልዩ ልዩ የግል ገቢ ማግኛ ሥራዎች? ከቅጥር ደመወዝና ከማናቸውም የሥራ ግንኙነቶች…ወዘተ፡፡ ይህ በየትም ስፍራ ያከናውኗቸውንና የተሳተፉባቸውን አጠቃላይ የገቢ ማግኛ የሥራ እንቅስቃሴዎችዎን ሁሉ ይመለከታል፡፡
ይኼ የመግቢያ ጥያቄ ብቻውን ተመሳሳይ የምርመራ ጠባይ ያላቸውን ሌሎች አስራ ሶስት ዝርዝር ጥያቄዎችን ያስከትላል፡፡ ደግሞ የጥያቄዎቹ የወዳጅነት ባህሪ ደረጃስ…! ለምሳሌ በገጠር መንገድ  የሽፍትነት፣የስርቆት ተግባር አሊያም ለእሳት አደጋ መንስኤነት ተጋልጬ እንደሁ ወይም ደግሞ በመግቢያው ንዑስ ጥያቄ ውስጥ በገቢ ማግኛነት እንድገልፃቸው ከተጠየቅኩት በተለየ መልኩ በአንዳች ልዩ የገቢ ማግኛ ምስጢራዊ እንቅስቃሴ ውስጥ ተሳትፌም ሆነ በህገ ወጥ መንገድ ካልታወቀ ሦስተኛ አካል ማንኛውንም አይነት ንብረት ተረክቤ እንደሆነ ለማወቅ ተለሳልሰው ምላሽ ለማግኘት የሚያግባቡ ጥያቄዎች ናቸው፡፡
መቼም ያ እንግዳ ሰውዬ በራሴ ላይ እንዳሾፍ አድርጎ እንዳሞኘኝ በፍፁም አልክድም፤በነፍሴ እንደተጫወተብኝ ግልፅ ነው፡፡ ያገጠጠ መጃጃል! አሁንም አፈላልጌ ሌላ ሻል ያለ ጠንቋይ ቀጠርኩ፡፡ ዋ! አጉል ክብር ፍለጋ ስንጠራወዝ እንግዳው ሰው በሁለት መቶ አስራ አራት ሺህ ዶላር የአመት ገቢ የእምነት ክህደት ቃሌ ሸብቦኝ እብስ ብሏል፡፡ በህጉ መሰረት እስከ አንድ ሺህ ዶላር የአመት ገቢ ከሥራ ግብር ነፃ ነው፡፡ በቃ ይኸው ብቻ ነው እስካሁን የታየኝ፡፡ እና ይኸ ምኑ መፍትኼ ይሆናል? ከሰፊ ውቅያኖስ በእፍኝ የመጥለቅ ያክል ነው፡፡ እነሆ በህጉ መሰረት ልከፍል ከሆነ’ኮ እንግዲህ ሳልጠየቅ ከተናዘዝኩት አምስት ከመቶው ሲሰላ፣አስር ሺህ ስድስት መቶ ሀምሳ ዶላር የመንግስት ዕዳ እላዬ ላይ ያናጥርብኛል ማለት ነው!
(እንዴ! ቆይ ግን እንዲህ ብልስ በቃ…ይኼንን ያህል ገቢ አላስገባሁም፡፡)
አንድ የናጠጠ ዲታ ሰው አውቃለሁ፡፡ የመኖሪያ ቤቱ የጊቢ ስፋት ፈረስ ያስጋልባል፤እልፍኙ የቤተመንግስት፤የምግብ ጠረጴዛው ግብር የሚያበሉበት አይነት የትየለሌ፣ የቤት ወጪው እልፍ አዕላፍ፤ ሆኖም ደግሞ ምናምኒት የሌለው፤ ችግር ያቆራመደው ድሀ ነው፡፡ በግብር ከፋይ ዜጎች ሥም ዝርዝር ላይ በየአመቱ የሚከፍለውን የግብር መጠን ብዙ ጊዜ የማየት ዕድል ገጥሞኝ ያውቃል፡፡ ስለዚህም ከጠፈነገኝ ማነቆ እላቀቅ ዘንድ ምክሩን እንዲለግሰኝ ወደ እርሱ  ሄድኩ፡፡
ባለፀጋው ሰው ቅፆቹን ተቀበሎኝ፣ የንባብ መነፅሩን ሰክቶ ብዕሩን ባነሳበት ቅፅበት በድንገት መናጢ ደሀ ሆኜ ቁጭ አልኳ! መቼም እንዲህ ያለ እንከን የለሽና ፅድት ያለ የሒሳብ ቀመር ተሰርቶ አይቼም አላውቅ፡፡ በቃ በሚገርም ብልሀት ገቢዬን ጎማምዶ፣ ወጪዬን ቆልሎ ትርፌን እያቀናነሰ በቀላሉ ኮቸመልኝ፡፡ የሀገር ውስጥ ገቢ፡ የ‹ክልል›፣የከተማ መስተዳድር፡ የ‹ወረዳ›፣ወዘተ እያለ የቀረጥ አይነቶች ቀጥሎ ቀጣጥሎ እና የቻለውን ያህል የወጪዎች መአት ደርድሮ ከተበልኝ፡፡ በተለይ የሚያንገበግቡ እጦቶቼን…‹‹በመርከብ መስጠምና በእሣት ቃጠሎ አደጋዎች ያጣሁዋቸው አንጡራ ሀብቶቼ!›› ከሁሉም በላይ ደግሞ ‹‹የቤት ንብረቶቼን ስሸጥ የደረሰብኝ ታላቅ ኪሳራ›› ፤ ‹‹የቤት እንስሳቶቼንም መሸጤ!›› እናም ‹‹የተቆለለብኝን የቤት ኪራይ እዳ ተሟሙቼ መክፈሌ!›› እያለ ደርድሮ  ኮለኮላቸው፡፡ ‹‹በተረፈ ሌሎቹ ገቢዎቼ ሁሉ በደንቡ መሰረት ባግባቡ የተቀረጡ ስለመሆናቸውም፤በዩናይትድ ስቴትስ የጦር ሠራዊት አባልነቴ የሚከፈለኝ ደመወዜም ሆነ በሌሎች ማናቸውም አይነት የሥራ ግንኙነቶቼ የሚከፈሉኝ ሁሉ›› ብሎ ፃፈልኝ፡፡
በተለይ መከራና ሰቆቃዎችን በተመለከተ ሌሎችንም ብዙ ብዙ ህይወቴን ሙልጭ ያወጡ ተግዳሮቶቼን በቅፁ ላይ አስፍሮልኛል፡፡ ለእያንዳንዱ የቅፆቹ መጠይቆች አስፈላጊውን ምላሽ በበቂ ምክንያት እያስደገፈ አስደናቂ ‹‹ቅነሳ›› እና ክርከማ አድርጎ አስልቶ ሲጨርስ ወረቀቶቹን መዳፌ ላይ አኖረልኝ፡፡ ቅፆቹን ለማየት ጊዜ አላጠፋሁም፡፡ እ…ሺ…እና አሁን ከአጠቃላይ የአመት ገቢዬ የተጣራ ትርፌ ስንት ሆኖ ተገኘ ? አንድ ሺህ ኹለት መቶ ሀምሳ ዶላር ከአርባ ሳንቲም ብቻ!
‹‹እንግዲህ…›› አለ ‹‹እንደሚታወቀው በሥራ ግብር አፈፃፀም ህጉ መሰረት አንድ ሺህ ዶላሩ ከሥራ ግብር ነፃ ነው፡፡ አሁን ካንተ የሚጠበቅ ነገር ቢኖር፤ ቅፆቹን ይዘህ ሄደህ መሀላህን ትፈፅምና ከሁለት መቶ አምሳ ዶላር ገቢህ ላይ የሚጣልብህን የሥራ ግብር መክፈል ብቻ ነው›› አለኝ(እሱ ለኔ ይሄንን እያለኝ፤ ትንሹ ልጁ ዊሊ ከአባቱ ኪስ ሁለት ዶላሮችን መዝዞ አውጥቶ ሹልክ አለ፡፡ እንዲህ ስል አሰብኩ…  መቼም ያ የተረገመ እንግዳ ነገ ዊሊንም አግኝቶ ጥያቄ ቢያቀርብለት፤ ዊሊ ስለ ገቢው ጉዳይ ሽምጥጥ! አድርጎ እንደሚክደው እርግጠኛ ነኝ፡፡)
‹‹እንደው ለመሆኑ ጌታው›› አልኩት  ‹‹ሌላም ጊዜ የየትኛውንም ስራዎችህን ገቢዎች ሁሉ እንዲህ ባለ መልኩ አራቁተህ ማለቴ ቀናንሰህ ነው የምታሳውቀው ማለት ነው?››
‹‹እንክት! ‹ወጪዎች› በሚል አርዕስት ስር እነዚህ አስራ አንድ ጥያቄዎች በቅፁ ላይ ያልተካተቱ ቢሆኑ ኖሮኮ፤ በየአመቱ ሀብቴ እየቆረቆዘ እመነመነ ወርዶ ወርዶ ነጫጭባ ድኃ ሆኜ ቀርቼ ነበር፡፡ ህእ! ምን በወጣኝ ነው ለዚህ ጨካኝ! ግፈኛ! አረመኔ! አምባገነን መንግስት በግብር ስም ገንዘቤን የማስታቅፈው?!›› አለኝ ባለፀጋው፡፡
ይህ ባለፀጋ ሰው፤በከተማችን ውስጥ አሉ ከሚባሉት ስመ ገናና ሀብታሞች መካከል በዋነኝነት የሚጠቀስ ነው፡፡ በሰው ልጅ የበጎ ሥነ-ምግባር መለኪያም በንግድ ሞያቸው በኩል በተዓማኒነት ከሚወደሱት፤በማህበራዊ ህይወት ተሳትፏቸውም እንከን የማይወጣላቸው ከሚባሉት ተርታ የሚመደብ፡፡ ታዲያ እኔስ ምኔ ሞኝ---የዚህን የተከበረ ዲታ ምክርና ብልሃት የማልመራበት?
ወደ ግብር መክፈያው ቢሮ ሄድኩ፡፡ እናም በትዝብት አፍጥጠው በሚያዩኝ የዚያ የእንግዳዬ ሰው አይኖች ፊት ‹‹አይኔን በጨው አጥቤ›› ቆሜ፤ በሀሰት ላይ ሀሰት እያነባበርኩ ሽምጥጥ አድርጌ ክጄ መሀላ ፈፀምኩ፡፡ የውሸት መአት! የቅጥፈት መአት! የክህደት መአት! የማስመሰል መአት! ግብሬ እየቀነሰ … እየቀነሰ … እየቀነሰ በሔደ መጠን፤እኔም ቁልቁል እየወረድኩ…በመንፈስ ልዕልናዬ እየጎደፍኩ… እየዘቀጥኩ… እየዘቀጥኩ እሄድ ጀመር፤ከራሴ ህሊና ጋር መልሼ ወደማልታረቅበት የክብረ-ቢስነት አዘቅት፡፡

Published in ጥበብ

    ክብደትን መቀነስ የልብ በሽታን ለማስወገድ ትክክለኛውመንገድ ነው፡፡ ከፍተኛ የሰውነት ክብደት የደም ቅዳ ሴሎቻችን እንዲጠቡ ያደርጋቸዋል፡፡ በዚህ ሳቢያም የኮሌስትሮል ዝቃጮች እንዲሰበሰቡና እጢ እንዲፈጠር ያደርጋል፡፡ ይህ ደግሞ አደገኛ የልብ ህመም እንዲከሰትብዎ ምክንያት ይሆናል፡፡ ክብደትዎን በመቀነስ በተለይም የሆድ አካባቢ ቦርጭዎን በማጥፋት የደም ቅዳ ሴሎች ሥራቸውን በአግባቡ እንዲያከናውኑ ይርዱዋቸው፡፡

         የምግብዎን ዓይነት እና መጠን ያስተካክሉ

    ለመልካም ጤንነት ከሚመከረው የምግብ ዓይነትና መጠን በላይ መመገብ ለከፍተኛ የሰውነት ክብደትና የኮሌስትሮል መጠን ያጋልጣል፡፡ የሚመገቡት ምግብ በዓይነቱና በመጠኑ የተስተካከለ እንዲሆን ያድርጉ፡፡ ከየዕለታዊ  የምግብ ገበታዎ ላይ አትክልትና ፍራፍሬዎች መኖራቸውን ያረጋግጡ፡፡ ገበታዎ የተመጠነ እንዲሆንም ያድርጉ፡፡
ጭንቀትዎን ያስወግዱ
ከፍተኛ ጭንቀት የደም ግፊት ይጨምራል፡፡ በደም ቅዳዎች ውስጥ እጢ እንዲፈጠር የሚያደርጉ ነገሮችንም ያባብሳል፡፡ ይህም ለልብ በሽታ ያጋልጣል፡፡ ከልብ በሽታ ለመጠበቅ ከፈለጉ ጭንቀትና ውጥረትን ያስወግዱ፡፡
ያልተፈተጉ/ ገለባቸው ያልተለየ/ እህሎችን ለምግብነት ይምረጡ
ገለባው ያልተነሳላቸውት (ያልተፈተጉ/እህሎች ጥሩ የአሰርና የሌሎች አልሚ ምግቦች ምንጮች ናቸው፡፡
    እንደ ቫይታሚን ኢ፣ ታያሚን፣ ሪቦፍላቪንና ናያሊን ያሉ ቫይታሚኖች እንዲሁም ማግኒዚየም፣ ፎስፈረስ፣ ዚንክና ብረት መሰል ማዕድናት የሚገኙት ባልተፈተጉ እህሎች ውስጥ ነው፡፡ ባልተፈተጉ እህሎች ውስጥ የሚገኙት ቫይታሚኖችና ማዕድናት፣ የደም ግፊትንና የልብ ጤንነትን በመቆጣጠሩ ረገድ የሚጫወቱት ሚና ከፍተኛ ነው፡፡ ከእነዚህ መካከል ለምሳሌ ለመጥቀስ ያህል ካልተፈተገ ገብስ ወይም ስንዴ የተሰሩ ዳቦዎች፣ ቡናማ ሩዝ፣ ካልተፈተገ በቆሎ የሚሰሩ ምግቦች ተጠቃሽ ናቸው፡፡
አነስተኛ የስብ መጠን ያላቸውን የፕሮቲን ምንጮች ይምረጡ
ቀይ ሥጋ፣ ዶሮና ዓሳ አነስተኛ የስብ መጠን ያላቸው የፕሮቲን ምንጮች ናቸው፡፡ የእንቁላል ነጩ ክፍል፣ የወተት ተዋፅኦዎችም ከአነስተኛ የስብ መጠን ውስጥ የሚመደቡ ናቸው፡፡ ዓሣ አነስተኛ የስብ መጠን ያለው የፕሮቲን ምንጭ ነው፡፡ የተወሰኑ የዓሣ ዓይነቶች ደግሞ የደም ውስጥ ስቦችን በመቀነስ በድንገተኛ የልብ ህመም የመሞት አደጋን በሚቀንሱትና ኦሜጋ 3 ፋቲ አሲድ ተብለው በሚታወቁ ማዕድናት የበለፀጉ ናቸው፡፡ ሌሎች ኦሜጋ 3 ፋቲ አሲዶች ምንጮች አኩሪ አተርና ተልባ ናቸው፡፡
በምግብ ውስጥ የሚኖረውን የጨው መጠን ይቀንሱ
ብዙ ጨው መመገብ ለከፍተኛ የደም ግፊት አስተዋፅኦ በማድረግ ለስርዓተ ልብ መዛባት ችግር ያጋልጣል፡፡ በምግባችን ውስጥ የሚገኘውን ጨው መቀነስ ጤናማ ልብ እንዲኖረን ከሚረዳን የአመጋገብ ሥርዓት ውስጥ ዋንኛው ነው፡፡ አንድ ጤናማ ሰው በቀን ውስጥ መውሰድ የሚኖርበት የጨው መጠን ከአንድ የሻይ ማንኪያ መብለጥ የለበትም፡፡
ኦቾሎኒ ለልብ ጤንነት
እንደ መክሰስ ያለ ነገር ካማረዎ፣ ኮሌስትሮል በመቀነስ የታወቀውን ኦቾሎኒ ይጠቀሙ፡፡
ኦቾሎኒ ጉዳት በማያስከትሉ ስቦች የተሞላና ጎጂ ስቦችን ከሰውታችን በማስወገድ የሚታወቅ ምግብ ነው፡፡     በርካታ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት፤ በየዕለቱ ጥቂት ኦቾሎኒን የሚመገቡ ሰዎች ከልብ በሽታ የመያዝ ዕድላቸው በእጅጉ ቀንሶ ተገኝቷል፡፡ ኦቾሎኒ በከፍተኛ ስብና ካሎሪ የተሞላ ስለሆነ በአንድ ጊዜ ከአንድ እፍኝ  በላይ አይጠቀሙ፡፡ በስኳር ወይም በቸኮሌት ጣፍጠው ከተዘጋጁ ኦቾሎኒዎች ይጠበቁ፡፡
የአካል እንቅስቃሴ ያድርጉ
በሳምንት ለ5 ቀናት በቀን ለ30 ደቂቃ ያህል ቀለል ያሉ የአካል እንቅስቃሴዎችን ያድርጉ፡፡ እንደ ኤሮቢክስ ያሉ ወይንም የልብን ጡንቻዎች ለማሰራት ይጠቅማሉ እንደሚባሉት የእግር ጉዞ አይነት እንቅስቃሴዎች በልብ ድካምና በሌሎች የልብ በሽታዎች የመጠቃት ዕድልን ይቀንሳሉ፡፡ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች በበዙ ቁጥር ጠቀሜታቸውም በዚያው ልክ እየጨመረ ይሄዳልና፣ በየዕለቱ አካላዊ እንቅስቃሴ ያድርጉ፡፡

Published in ዋናው ጤና

  የታይፎይድ አምጪ ባክቴሪያ የሚከሰተው በሰው ላይ ብቻ ነው
            ለበሽታው የሚታዘዙ አብዛኛዎቹ መድኀኒቶች ከበሽታው ጋር ተላምደዋል
    አብዛኛውን ጊዜ በተበከለ ምግብና ውሃ ሳቢያ ከሰው ወደ ሰው የሚተላለፈውና በተለምዶ የአንጀት ተስቦ እየተባለ የሚጠራው ታይፎይድ መነሻው “ሳልሞኔላ ታይፊ” የሚባል ባክቴሪያ ነው፡፡ ይህ ባክቴሪያ የሚኖረው (ህይወት የሚያገኘው) በሰው ልጅ አንጀት ውስጥ ብቻ ነው፡፡
በሽታው በሽታ አምጪ በሆነው ባክቴሪያ በተበከለ ምግብና መጠጥ አማካኝነት በወረርሽኝ መልክ ሊከሰት ይችላል፡፡
በበሽታው የተያዘ ሰው በጥቂት ቀናት ውስጥ ምልክቶችን ማሳየት ይጀምራል፡፡ ከበሽታው ምልክቶች መካከል ትኩሳት ዋንኛው ሲሆን ራስ ምታት፣ ሰውነትን የመቀረጣጠፍና መገጣጠሚያ አካባቢ የሚኖር የህመም ስሜት ከምልክቶቹ መካከል የሚጠቀሱ ናቸነው፡፡
እ.ኤ.አ በ1862 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩትን 16ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት አብርሃም ሊንከን ለሞት ማብቃቱ የሚነገርለት ታይፎይድ አሁንም በዓለማችን በየዓመቱ ከ220 ሺህ በላይ ሰዎችን ለሞት እየዳረገ ይገኛል፡፡
ከጥቂት የሰሜን አፍሪካ አገራትና ከደቡብ አፍሪካ በስተቀር በመላው የአፍሪካ አገራት በስፋት መኖሩ የሚነገረው የታይፎይድ በሽታ በተለይ የሃሞት ከረጢት እና እጢ ያለባቸው ሰዎች በይበልጥ ያጠቃል፡፡ ባክቴሪያው ከአንጀት ውስጥ በደም ተሸካሚነት ወደ ሃሞት ከረጢት ሊሄድና በዚያ ተደብቆ ህመምተኛውን ሊያጠቃና በሰገራ አማካኝነት ወደሌሎች ሰዎች ሊተላለፍ ይችላል፡፡
ሳልሞኔላ ታይፊ በሚባል ባክቴሪያ ሳቢያ የሚከሰተውን ይህንኑ የታይፎይድ በሽታ ለማከም ጥቅም ላይ የሚውሉት መድኀኒቶች በአብዛኛው ከበሽታው ጋር የመላመድ ባህርይን አምጥተዋል፡፡
ቀደም ሲል በጥቅም ላይ ይውሉ የነበሩና የታይፎይድ በሽታን ለማከም ያገለግሉ ከነበሩ መድኀኒቶች መካከል አሞክሳሲሊን፣ ክሎሞፌኒከልና፣ ስትሬፕቶማይሰን የተባሉት መድኀኒቶች ሙሉ በሙሉ ከበሽታው ጋር በመላመዳቸውና የሚያስከትሉት የጎንዮሽ ጉዳቶችም እየጨመሩ በመምጣታቸው ከአገልግሎት ውጪ እንዲሆኑ እየተደረጉ ነው፡፡
 በአሁኑ ወቅት አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኘው ሲፕ ሮፋሎክሳሲን የተባለው መድኀኒት ነው፡፡
በሽታው በወቅቱ ህክምና ካላገኘ ለሞት ሊዳርግ የሚችልና በቀላሉ ከሰው ወደሰው በተበከለ ምግብና መጠጥ ሳቢያ ሊተላለፍ የሚል በሽታ ነው፡፡
 በተለይ እንዲህ ክረምት በሚሆንባቸው ወቅቶች ለመጠጥነት የምንጠቀመውን ውሃና የምንመገበውን ምግብ በጥንቃቄ መያዙ በታይፎይድ ከመያዝ እንደሚታደገን ባለሙያዎች ይመክራሉ፡፡

Published in ዋናው ጤና

 አፍሪካ ኢንቨስተሮች መሳቧን ቀጥላለች
                         
   በርካታ የበለፀጉ የአሜሪካና የአውሮፓ ኢንቨስተሮች ለኢኮኖሚያቸው ማደግና ለህልውናቸው መቀጠል አፍሪካን ተስፋ እያደረጉ ነው፡፡ ለምን መሰላችሁ? እንደቀድሞው በአገራቸው ብቻ ቢወሰኑ ዓመታዊ ዕድገታቸው ከ2 ወይም ከ3 በመቶ አይበልጥም፡፡ በዓለም ከፍተኛ ዕድገት እየተመዘገበ ያለው በአፍሪካና በሩቅ ምስራቅ አገሮች ነው፡፡ አንዳንድ አገሮች በሁለት አኀዝ ብዙዎቹ ደግሞ ከ5 በመቶ በላይ እያደጉ ነው፡፡ ስለዚህ በእነዚህ አገሮች ኢንቨስት ማድረግ ያዋጣል፡፡ የዓለም 10 ምርጥ ዝነኛ ባለ 5 ኮከብ ሆቴሎች በአፍሪካ ኢንቨስት ለማድረግ መወሰናቸውን ባለፉት ጥቂት ሳምንታት አስነብበናችኋል፡፡ ባለፈው ሳምንት ማርዮት፣ ሂልተን ኢንተርናሽናል፣ ራዲሰን ብሉ፣ … በሩዋንዳና በሌሎችም አገሮች አዳዲስ ሆቴሎች ለመገንባትና ያሉትንም በማስፋፋት እየተንቀሳቀሱ መሆኑን ነግረናችኋል፡፡ ለአብነት በአገራችን ያለውን ብናይ ማሪዮት ሆቴል በኢትዮጵያ ሦስት ሆቴሎች እየሰራ ነው፡፡
አንደኛው እስጢፋኖስ ቤተክርስቲያን አካባቢ የተሰራው ቢዘገይም በቅርቡ ተመርቆ አገልግሎት እንደሚጀምር ከውስጥ አዋቂዎች ሰምተናል፡፡ ሁለተኛው ቦሌ መድኀኒዓለም ቤተክርስቲያን አካባቢ፣ ሦስተኛው በሀዋሳ ከተማ እየተሰራ ነው፡፡ ሂልተን ኢንተርናሽናልም ግንባታው ዘገየ እንጂ (ኧረ ቆሟል ማለት ይሻላል) በማስፋፊያ ከኢምፔሪያል ሆቴል ፊት ለፊት ወይም ከኢትዮጵያ ወጣቶች ስፖርት አካዳሚ ጀርባ ሁለተኛ ሆቴል እየሰራ መሆኑ ተነግሯል፡፡
አሁን ደግሞ በአፍሪካ ኢንቨስት የማድረግ ፍላጎት የአረብ ባለሀብቶች ተራ ነው፡፡ በመጪው ሳምንት ቅዳሜና እሁድ እዚሁ በሸራተን ሆቴል የአረብ- አፍሪካ ሕግ አውጪዎችና ቢዝነስ ፎረም በአፍሪካ ኢንቨስት ማድረግ ትርጉም አለው (Investing in Africa Makes Sense) በሚል ርዕስ እንደሚወያዩ ፓን አፍሪካን ቻምበር ኦፍ ኮሜርስ ኤንድ ኢንዱስትሪ አስታውቋል፡፡
የአረብና የአፍሪካ አገሮች የቢዝነስ ትብብር ፎረም አዲስ አይደለም፡፡ የአፍሪካና የአረብ ዓለም ሴኔቶች ሹራና ተመሳሳይ ደረጃ ያላቸው ም/ቤቶች ማኅበር (ኤሴካ) ከተመሰረተ ቆይቷል፡፡ በንግድ ጉዳዮችና በሌሎም የትብብር ማዕቀፎች ተወያይተው ያውቃሉ፡፡ የአሁኑ ፎረም ያስፈለገው ሁለቱም አኅጉሮች አንዱ ከሌላው የሚፈልገው ነገር ስላለ ነው፡፡ አፍሪካ ለኢንቨስትምነት አመቺና በዕድገት ጎዳና ላይ ብትሆንም መዋለ ነዋይ በጣም ያስፈልጋታል፡፡ የአረብ አገራቱ ደግሞ ያለሥራ የተከማቸ የዘይት ዶላር አላቸው፡፡ ሁለቱን አቀናጅቶ መስራት በማስፈለጉ የፓን አፍሪካን ቻምበር ኦፍ ኮመርስና ኢንዱስትሪ (ፒፓሲ.ሲሲአይ) እና (አሴካ) በጋራ ይህን ፎረም ማዘጋጀታቸው ታውቋል፡፡
ማንም ኢንቨስተር ቢሆን ገንዘቡን አውጥቶ ኢንቨስት ሲያደርግ ከአቅም በላይ ካልሆነ በስተቀር መክሰር አይፈልግም፤ ዋስትና ይፈልጋል፡፡ ፎረም የአፍሪካና የአረብ አገሮች እንዴት መሥራት እንዳለባቸው ለህግ ጉዳዮች እልባት ያበጃል፡፡ በፎረሙ የሴኔትና የሹራ አባላት ከቢዝነስና ኢንቨስትመንት ማህበረሰቦች ማህበራት፣ የንግድ ም/ቤቶች፣ የኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን ጽ/ቤት ባለሙያዎች፣ የቢዝነስ መሪዎችና ሀሳብ አፍላቂዎች፣ ዋና ዋና ኢንቨስተሮችና የመንግሥት ውሳኔ ሰጪዎች አሁን በአፍሪካና በአረብ አገራት መካከል ያለውን የንግድ መጠን ከሦስትና ከአምስት እጥፍ በላይ እንዴት ማድረስ ይቻላል በሚል የፖሊሲ ምክክር ያደርጋሉ፡፡
አፍሪካ፣ ከዓለም የነዳጅ ድፍድፍ ያላት 12 በመቶ ያላት ሲሆን፣ የወርቅ ክምችቷ ደግሞ 42 በመቶ ነው፡፡ በምስራቅ የአኅጉሪቷ ክፍል የተገኘው በርከት ያለ የተፈጥሮ ጋዝ ክምችት የአህጉሩ የኢኮኖሚ አቅም እንዲጨምር አድርጓል፡፡ አፍሪካ፣ አዲስ የዕድገት ዋልታ ስለሆነች በማንኛውም ዘርፍ፣ የመሰረተ ልማት፣ የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ፣ የችርቻሮ ንግድ፣ በጤና ዘርፍ በማኑፋክቸሪንግ፤ … ኢንቨስት ቢያደርጉባት ከማንኛውም የዓለም ክፍል የተሻለ ከፍተኛ ጥቅም እንደሚገኝባት የፎረሙ አዘጋጆች ያምናሉ፡፡
በሌላ በኩል ደግም በነዳጅ ኃይል ምንጭነት የበለፀጉ የገልፍ አገሮች የትብብር ምክር ቤት ከፍተኛው የነዳጅ ሽያጭ (አሁን ቢቀንስም) ያከማቸለት የተትረፈረፈ ካፒታል አለው፡፡ ከአፍሪካ አገራት ጋር ዋነኛ የንግድና ኢንቨስትመንት ትስስር ያላቸው አገሮች ዱባይና የተባበሩት የአረብ ኢመሬትስ ብቻ እንደሆኑ ጥናቶች ያመላክታሉ፡፡ ጥሩ ማሳያ የሚሆነው በቅርቡ በዳንጎቴ ሲሚንቶ ፋብሪካና በዱባይ ኢንቨስትመንት ኮርፖሬሽን ጋር የተደረገው የ300 ሚሊዮን ዶላር ትብብር ስምምነት ነው፡፡
በተመሳሳይ ወር፣ የኳታር ብሄራዊ ባንክ ከትራንስናሽናል ኢኮ ባንክ ድርሻ መግዛቱ ነው፡፡ የዱባዩ ኢንቨስትመንት ኮርፖሬሽን በዚህ ዓመት መጀመሪያ ከደቡብ አፍሪካ ሆቴል ማናጀር Kerzner International የአክሲዮን ድርሻ ገዝቷል፡፡ ሌሎች በርካቶችም በግል ሀብትና በልማት ብድር በአፍሪካ አህጉር ኢንቨስት ማድረጋቸው ታውቋል፡፡
በምግብ ሰብል ራስን ለመቻል በእርሻው ዘርፍ የሚደረገውን ጥረት ወደ ላቀ ደረጃ ማሳደግ የሚቻልበት መንገድ ሰፊ ነው፡፡ ሌላስ በአፍሪካና በአረብ አገሮች መካከል የሚደረገው ትብብር ማሳደግ የሚቻልበት መንገድ ይኖር ይሆን? አዘጋጆቹ በአፍሪካና በአረብ አገሮች መካከል ሊኖር የሚገባው አዲስ የረዥም ጊዜ ትብብር በፎረሙ ውይይት ወቅት ይነሳል የሚል እምነት አላቸው፡፡
የአፍሪካን የውጭ ኢንቨስትመንት ዕድገት መጠን (ኤፍዲአይ) ለማሳደግ ምን መደረግ አለበት? የሚለው ሌላው የፎረሙ መወያያ ርዕስ ነው፡፡ በ2013 ዓ.ም 1.9 ትሪሊዮን ዶላር የነበረው የአህጉሩ አጠቃላይ ጂዲፒ አሁን ከብራዚል ወይም ከሩሲያ እኩል ስለሆነ አፍሪካ ከዓለም አገራት በፍጥነት እያደገ ያለ ኢኮኖሚ ባለቤት ሆናለች፡፡
የቢዝነስ ፍላጎት ከአመቺ የቢዝነስ ሁኔታ ጋር የተቆራኘ ስለሆነ ቀደም ሲል በአፍሪካ ኢንቨስት ለማድረግ ይፈሩ የነበሩትን ኩባንያዎች ሁሉ በአፍሪካ ኢንቨስት እንዲያደርጉ እየገፋፋቸው ነው፡፡ የአፍሪካ ገበያዎች እንደ አሜሪካ፣ ቻይናና ምዕራብ አውሮፓ አገሮች ካሉ አስቸጋሪ ግዙፍ ገበያዎች የተሻለ ቢሆንም አሁንም እጅግ በርካታ ስጋቶች አሉበት፡፡
ለአፍሪካ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መቀጨጭ ብዙ ምክንያቶች ቢጠቀሱም ዋነኞቹ እርግጠኛ ያለመሆን ወይም የፖለቲካና የማክሮ ኢኮኖሚ ያለመረጋጋት፣ ግልጽ ፖሊሲ ያለመኖር፣ የጂዲፒ ዕድገትና የገበያ መጠን ማነስ፣ የመሰረተ ልማት እጥረት፣ ለአገር ውስጥ ኢንዱስትሪዎች የሚደረግ ከፍተኛ ከለላ፣ ከፍተኛ የሸቀጣ ሸቀጥ ጥገኝነት፣ የፉክክር ክፍተትና ሙስና፣ ደካማ አስተዳደር እንዲሁም ደካማ የገበያ ስትራቴጂ…. መሆናቸውን አዘጋጆቹ ጠቅሰው፣ በእነዚህ ነጥቦች ላይ በማተኮር ውይይት እንደሚካሄድ አመልክተዋል፡፡

Page 2 of 17