መቀመጫውን በስዊዘርላንድ፣ጄኔቫ ያደረገው የተባበሩት መንግሥታት የንግድ ለልማት ጉባኤ (አንክታድ)፣የአፍሪካ ቢሮውን በአዲስ አበባ የከፈተ ሲሆን ቢሮው የተከፈተው  የጉባኤው አባል አገራትን በቀጥታና በቅርበት ለማገልገል ታቅዶ ነው ተባለ፡፡
የጉባኤው ዋና ጸሐፊ ዶ/ር ሙኪሳ ኪቲዩ ባለፈው ረቡዕ በመክፈቻ ሥነስርዓቱ ላይ  እንደተናገሩት፤ የጉባኤው የአፍሪካ ቢሮ በአዲስ አበባ መከፈት ለመንግስት ፖሊሲ አውጪዎችና ተቋማት በቅርበት ድጋፍ ለመስጠት ያስችለዋል፡፡ ኢትዮጵያ አንክታድ ሰፊ እንቅስቃሴ ከሚያደርግባቸው ሶስት የአፍሪካ አገራት አንዷ መሆኗና የበርካታ ዓለም አቀፍ ተቋማት መቀመጫነቷ ቢሮውን በአገሪቱ ለመክፈት ተመራጭ አድርጓታል ተብሏል፡፡  
ጉባኤው በንግድ፣ ኢንቨስትመንትና ልማት ጉዳዮች ላይ የሚንቀሳቀስ ሲሆን ንግድ ሚኒስቴር፣ ማዕከላዊ ባንክና ገቢዎችና ጉምሩክን ጨምሮ ከተለያዩ አካላት ጋር ያለውን ቅርበት በማጠናከር እንደሚሰራ ታውቋል፡፡  
ጉባኤው በተለያዩ ጊዜያት በሚያወጣቸው ሪፖርቶች አማካይነት ለአባል አገራት የንግድና ኢንቨስትመንት ምክረ-ሃሳቦችን እያቀረበ እንደሚገኝ የገለፁት ዶ/ር ሙኪሳ፤ የቢሮው በኢትዮጵያ መከፈት በአፍሪካ አገራት ላሉ ተቋማት የቴክኒክና መሰል ድጋፎችን ለማድረግ ያስችለዋል ተብሏል፡፡  

 - በዘርፉ የሚነሱ ችግሮችን ይፈታል ተብሏል
                        

    የመጓጓዣ አውሮፕላኖችን የወንበር ገደብ ጨምሮ በግሉ የአቪየሽን ዘርፍ ላይ የሚታዩ አጠቃላይ ችግሮችን ይፈታል ተብሎ የሚጠበቅ ፖሊሲ፣ በያዝነው ዓመት መጨረሻ ተጠናቅቆ ተግባራዊ እንደሚሆን የትራንስፖርት ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ የሚኒስቴሩ የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ አሳልፈው አመዲን ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ በተሻሻለው የግል የአቪየሽን ፖሊሲ ላይ የፍትህ አካላት አስተያየት እንዲሰጡበት እየተደረገ ነው፡፡ የግል የአቪየሽን ዘርፍ አንቀሳቃሾች፤ የወንበር ገደብና ከ22 ዓመት በላይ የሰራ አውሮፕላን ወደ አገር ውስጥ እንዳይገባ የተቀመጠው ገደብ እንዲሁም በዘርፉ የሚታዩ መሰል ችግሮች ለስራቸው እንቅፋት እንደሆኑባቸው በተለያዩ ጊዜያት  ለሚኒስትሩ መስሪያ ቤት መግለፃቸውን ኃላፊው ተናግረዋል፡፡ የአቪየሽን ፖሊሲው በዘርፉ የሚነሱ ችግሮችን በመፍታት፣ውጤታማ ስራዎችን ሊያሰራ በሚችል መልኩ እየተዘጋጀ እንደሆነ የገለጹት ኃላፊው፤የባለሀብቱን እንዲሁም የአገሪቱን ጥቅምና ደህንነት የሚያስጠብቅ ይሆናል ተብሏል፡፡
 “ከዚህ ቀደም የወንበር ገደቡ ሲቀመጥ የግል አንቀሳቃሾች አቅምም አነስተኛ ነበር” ያሉት አቶ አሳልፈው፤አሁን የተነሳው ጥያቄ የዘርፉ ማደግና የአገሪቱ ልማት እድገት ውጤት ነው ብለዋል፡፡ የዘርፉ ተዋናዮች የሚያነሱት የጋራዥ ችግርም የአዲሱን ኤርፖርት መገንባት ተከትሎ የሚፈታ እንደሚሆን ሃላፊው ተናግረዋል፡፡  
የግል የአቪየሽን ኢንዱስትሪ አንቀሳቃሾች፣ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ የራሳቸውን ሚና እንዲወጡ ለማድረግ ፖሊሲው ጥያቄያቸውን መመለስ በሚያስችል መልኩ እየተሻሻለ እንደሚገኝ የጠቆሙት ኃላፊው፤ በአመቱ መጨረሻ የአፈፃፀም መመሪያ ተዘጋጅቶለት ወደ ስራ እንደሚገባ ገልፀዋል፡፡  

ሳምሰንግ ኤሌክትሮኒክስ ለምርቶቹ የጥገና አገልግሎት የሚሰጥበት የደንበኞች አገልግሎት ማዕከል በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ከፈተ፡፡
ለሳምሰንግ ሞባይልና ለሁሉም የሳምሰንግ ኤሌክትሮኒክ ምርቶች የጥገና አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል የተባለውንና በአዲስ አበባ ከተማ ቴሌ መድኀኒዓለም አካባቢ የተቋቋመውን የደንበኞች አገልግሎት ማዕከል ከትናንት በስቲያ መርቀው የከፈቱት የኩባንያው የኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጅ አቶ ታዲዮስ አወል ናቸው፡፡ ማዕከሉ ከጥገና በተጨማሪ (Software upgrades, application installation, new devises setup) አገልግሎቶችን ይሰጣል፡፡ አጠቃላይ የማማከር አገልገሎትም ለደንበኞቹ እንደሚሰጥ አቶ ታዲዮስ ተናግረዋል፡፡
ማዕከሉ የዋስትና ፈቃድ ላላቸውም ሆነ ለሌላቸው የሳምሰንግ ምርቶች አገልግሎቱን እንደሚሰጥ የጠቆሙት አቶ ታዲዮስ፤ ደንበኞች ጥራት ባላቸው የመለዋወጫ ዕቃዎች በሙያው በተካኑ ባለሙያዎች የህግና ሌሎች አገልግሎቶችን በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲያገኙ እንደሚደረግ ገልፀዋል፡፡
 እንደፍሪጅ እና የልብስ ማጠቢያ ማሽን ላሉና የትራንስፖርት ወጪን ለሚጠይቁ የሳምሰንግ ምርቶች የማዕከሉ የጥገና ባለሙያዎች ቤት ለቤት በመሄድ አገልግሎቱን እንደሚሰጡና ይህንንም አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተገልጿል፡፡

 አስደማሚ … አስገራሚ … አስደናቂ እውነታዎች!?
          የኬንያው ጠንቋይ፤ “ኦባማ የአባቱን አገር ይጎበኛል” ሲል ተነበየ
             “የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ይሆናሉ ብሎ ተንብዮ ነበር” (USA Today)
   ባራክ ኦባማ በፕሮግራም መጣበብ የተነሳ በኬንያ ቆይታቸው የአባታቸውን የትውልድ ሥፍራ (ኮጌሎ) ለመጎብኘት እንደማይችሉ እየተነገረ ቢሆንም ዕውቅ አንድ የኬንያ ጠንቋይ ፕሬዚዳንቱ የአያት ቅድመ አያቶቻቸውን አገር ይጎበኛሉ ሲል ሰሞኑን ተንብየዋል፡፡
ጆን ዲሞ የተባለው የኮጌሎ ጠንቋይ፤ ኦባማ በእርግጠኝነት የአባታቸውን የትውልድ ቀዬ እንደሚጎበኙ ታይቶኛል ብሏል፡፡ ኦባማ እስካሁን ኮጌሎን እንደሚጎበኙ ማረጋገጫ ባይሰጡም የመንደሩ ነዋሪዎች ግን አሁንም በተስፋ እየጠበቁ ነው፡፡ ስለዚህም ምናልባት ከመጡ በሚል ዝግጅታቸውን ቀጥለዋል፡፡
“እመኑኝ … ኦባማ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ይሆናል ብዬ ነበር፤ ሆነ፡፡ አሁንም የወላጆቹን የትውልድ ቀዬ የመጎብኘት ዕቅድ እንዳለው ታይቶኛል፡፡ ይመጣል፡፡” ሲል ተንብየዋል ዲሞ፡፡ ጆን ዲሞ እ.ኤ.አ በ2006 ዓ.ም ኦባማ ፕሬዚዳንት ይሆናሉ ብሎ መተንበዩን “ዩኤስኤ ቱዴይ” አስታውሷል፡፡ “ውጤቱ ኦባማ ኮጌሎ እንደሚመጣ ነው የሚጠቁመው፡፡ ይሄ ትልቅ ምስጢር ነው፡፡ የቅድመ አያቱን አገር እንደሚጎበኝ ለማንም መንገር የለበትም!” በማለት ጠንቋዩ በጉጉት ለተሞሉት የመንደሯ ነዋሪዎች ተናግሯል፡፡ ኦባማ በትላንትናው ዕለት ኬንያ የገቡ ሲሆን የሦስት ቀናት ጉብኝት ያደርጋሉ፡፡ በምዕራባዊ ኬንያ የሚገኘው የኮጌሎ መንደር፤ የአያቱ የሳራ ኦባማ የትውልድ ሥፍራ ሲሆን የአባቱ የባራክ ኦባማ (ሰር) የቀብር ስፍራም ያለው እዚያው ነው፡፡
           

  የዛሬ 8 ዓመት ኦባማ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሆነው መመረጣቸውን ተከትሎ በመላው ዓለም ዝናቸው በእጅጉ ናኝቶ ነበር፡፡ ለዚህም ይመስላል ከኬንያ የአባታቸው የትውልድ መንደር አንስቶ እስከ አየርላንድ ገጠር ድረስ ስማቸው ታዋቂ የሆነው፡፡ በተለይ በኬንያ በእሳቸውም ስም ያልተሰየመ ነገር ያለ አይመስልም፡፡ የአንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች፣ ኪዮስኮች፣ መደብሮች… ኧረ ህፃናትም አልቀሩ፡፡ ሁሉም የባራክ ኦባማን ስም የታደሉ ይመስላሉ፡፡ አንዳንድ በኦባማ ስም የተሰየሙ ነገሮች ደግሞ አግራሞትን የሚፈጥሩ ናቸው፡፡ ራሷ ኬንያ ኦባማ መባል ነው የቀራት፡፡ እስቲ Tuko.co.ke የተሰኘው ድረ-ገፅ በኦባማ ስም የተሰየሙ ነገሮችን በተመለከተ ያወጣቸውን መረጃዎች እናስቃኛችሁ፡፡

                “ኦባማ ተራራ”

   አንቲጓ የተባለችው የኬንያ ግዛት በኦባማ ስም የሚሰየም ትንሽ ነገር ያጣች ትመስላለች፡፡ በግዛቱ ያለ አንድ ትልቅ ተራራ በፕሬዚዳንቱ ስም ተሰይሟል፡፡ “ኦባማ ተራራ” ይባላል፡፡ “ቦZ ፒክ” በአንቲጓ በጣም ረዥሙ ተራራ ሲሆን ኦባማ የሚለው ስም የተሰጠው እ.ኤ.አ በ2009 በፕሬዚዳንቱ የልደት ቀን ነበር ተብሏል፡፡

            “ኦባማ ሹሩባ”

     ኦባማ ፀጉራቸውን ሹሩባ ተሰርተው ባያውቁም በአያቶቻቸው መንደር በኮጌሎ ግን አንድ የሹሩባ አሰራር በሳቸው ስም ተሰይሟል - “ኦባማ ሹሩባ” ተብሎ፡፡ አንዳንዶች “የወንዶች የፀጉር አቆራረጥ እንኳን ቢሆን ምንም አልነበር፤ ክፋቱ ግን ይሄ የፀጉር አሰራር ስታይል ያለው በሴቶች የውበት ሳሎን ነው…” ሲሉ ቅሬታቸውን ይገልፃሉ፡፡ የሰማቸው ወይም የሚሰማቸው ግን ያለ አይመስልም፡፡ በነገራችን ላይ በመዲናችን በሚገኙ የወንዶች ፀጉር ሴቶች የኦባማን ምስል (ፖስተር) በተለያዩ የፀጉር አቆራረጥ ስታይሎች ማየት የተለመደ ነው፡፡

             የአይሪሾቹ አልባሰም?! (“ኦባማ ነዳጅ ማደያ”)

      የኬንያውያን እንኳ እሺ… ምክንያት አላቸው፡፡ የአገራችን ልጅ ነው ቢሉ ያምርባቸዋል፡፡
የሚያስገርሙት አይሪሾች ናቸው፡፡ ድንገት ተነስተው እኮ ነው የኦባማን ስም የሙጥኝ ያሉት፡፡
ያውም በአየርላንድ እልም ያለ ገጠር መሃል፡፡ በዱብሊን እና ሊመሪክ መሃል ኦፋሊ ውስጥ የሚገኘው የነዳጅ ማደያ አሁን በይፋ በአሜሪካ ፕሬዚዳንት ስም ተሰይሟል፡፡ “ኦባማ ነዳጅ ማደያ” ነው የሚባለው፡፡ ይሄን እንኳን ራሳቸው ኦባማም የሚያውቁት አይመስለኝም፡፡

               የዬል ዩኒቨርሲቲ ሳይንቲስቶችስ?

   በአሜሪካ የሚገኘው የዬል ዩኒቨርሲቲ ሳይንቲስቶች ደግሞ ምን እንዳሰቡ አይታወቅም፡፡ ከምድረገፅ ጠፍቷል የሚባል ፍጡር በስማቸው ሰይመዋል ተብሏል፡፡ “ኦባማዶን” በዓለም ረዥሙ (አንድ ጫማ ርዝመት አለው) እንሽላሊት ሲሆን እንደ በቆሎ የተደረደሩ ጥርሶች እንዳሉት ሳይንቲስቶቹ ገልፀዋል፡፡ ለዚህ ተሳቢ ፍጥረት ስሙን ያወጡለት ሳይንቲስቶች እ.ኤ.አ በ2012 የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፣ ኦባማ ማሸነፋቸው በይፋ እስኪነገር ድረስ ዝም ብለው ሲጠብቁ ነበር፡፡ ለምን ቢባል… ድንገት ኦባማ ቢሸነፉ እንደ እንሽላሊቱ “ከምድረ ገፅ የጠፉ” የሚል በአግቦ ወይም በሾርኒ የተነገረ ስድብ እንዳይመስልባቸው ስለፈሩ ነበር፡፡

            አሁንስ አበዙት ያሰኛል!
    ይሄኛውስ ደስ አይልም፡፡ ኬንያውያን መካሪ የላቸውም እንዴ? ያሰኛል፡፡ የፀጉር ትሎች የተገኙት የኦባማ አባት የትውልድ ስፍራ በሆነችው ኮጌሎ መሆኑን የጠቆመው Tuko.co.ke የተሰኘው ድረ-ገፅ፤ እንደተለመደው አዲስ የተገኘው ትል በፕሬዚዳንቱ ስም ተሰየመ ይለናል፡፡ ለአሜሪካው መሪ ክብር ሲባልም የትሉ ሳይንሳዊ ስም “Paragordius Obamai” ተብሏል፡፡ ግን አይገርምም… የኦባማ ስም?! (ለአፍ ስለሚመች ይሆን?)   

 የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ከሆኑ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የአባታቸውን የትውልድ አገር ኬንያን በመጐብኘት ላይ የሚገኙት ባራክ ኦባማ፤ ትላንት Air Force One በተሰኘው ልዩ አውሮፕላናቸውን ኬንያ ገብተዋል፡፡
ከዋይት ሃውስ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ Air Force One የአውሮፕላን ስም አይደለም፡፡ የአሜሪካ ፕሬዚዳንትን የሚጭን ማንኛውም የአሜሪካ አየር ሃይል አውሮፕላን በዚህ ስም ነው የሚጠራው፡፡
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት በወታደራዊ አውሮፕላን  ላይ ከተሳፈሩ “Army One” ተብሎ ይጠራል፡፡ በልዩ ሄሊኮፕተራቸው ላይ ከተሳፈሩ ደግሞ አውሮፕላኑ “Marine one” ይባላል፡፡
ፕሬዚዳንቱ Air Force One በሚል ስያሜ የሚበሩ በልዩ ትእዛዝ የተሰሩ 2 ቦይንግ 747 ጀቶች ያሏቸው ሲሆን እኒህ ጀቶች የባለ 6 ፎቅ ህንፃ ከፍታ አላቸው ተብሏል፡፡
“Air Force One” በከፍተኛ ፍጥነት ሲበር በሰዓት 1ሺ 126 ኪ.ሜ ገደማ መጓዝ የሚችል ሲሆን አውሮፕላኑ በ45ሺ 100 ጫማ ከፍታ ላይ ነው የሚበረው፡፡ ተመሳሳይ የተጓዦች ቦይንግ 747 አውሮፕላን የሚበረው በ30ሺ ጫማ ገደማ ከፍታ ላይ ነው፡፡
አውሮፕላኑ አንዴ ነዳጅ ጢም ተደርጐ ከተሞላ (Full tank) የዓለምን አጋማሽ ማካለል የሚችል ሲሆን ዳግም ለመሙላት መሬት ላይ ማረፍ አያስፈልገውም፡፡ በአጋማሽ አየር ላይ ሆኖ ነዳጅ የመሙላት አቅም አለው፡፡ ከዚያም ይሄ ነው ለማይባል ጊዜ በአየር ላይ ሊቆይ ይችላል፡፡
የፕሬዚዳንቱ አውሮፕላን የአየር ጥቃት መቋቋም ይችላል፡፡ የእሳት ብልጭታ በመርጨት ሚሳየሎችን ከዒላማቸው ውጭ ከማድረጉም በተጨማሪ የጠላት ራዳርንም አገልግሎት አልባ ያደርጋል፡፡ ሌሎችም ለደህንነት ሲባል በምስጢር የተያዙ ገፅታዎች እንዳሉት ታውቋል፡
ግዙፉ የፕሬዚዳንቱ የአየር ላይ ቢሮ በሚል የሚታወቀው Air Force One  ለሰራተኞች፣ ለኃላፊዎችና ለእንግዶች የመኖሪያ ክፍሎች አሉት፡፡
በአውሮፕላኑ ውስጥ እጅግ ከሚያስደንቁ ገፅታዎች መካከል ብዛት ያላቸው የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎች ይጠቀሳሉ፡፡ አውሮፕላኑ ፕሬዚዳንቱንና ሰራተኞቹን በአየር ላይ ሆነው ከመላው ዓለም ጋር መገናኘት የሚያስችላቸው አስተማማኝ የስልክ መስመር ያለው ነው፡፡ ከተለያዩ የቢሮ እቃዎች በተጨማሪም 85 ስልኮች፣ 19 ቴሌቪዥኖች፣ ፋክስ ማሽኖችና ሬዲዮኖች ተገጥሞለታል፡፡
የፕሬዚዳንቱ አውሮፕላን 96 ተጓዦችና የበረራ ሰራተኞችን የመጫን አቅም አለው፡፡

                ለኦባማ በወንድና በሴት መካከል ያለውን ልዩነት እናሳያለን ይላሉ
  የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በስልጣን ዘመናቸው 11ኛ ሰዓት ላይ የፈቀዱት የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻ በአገራቸው ተቃውሞ አላስነሳባቸውም ይሆናል፡፡ በአባታቸው አገር ኬንያ ግን ተዝቶባቸው ነበር፡፡ ኦባማ በኬንያው ጉብኝታቸው የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻ መብትን የተመለከተ ጉዳይ እንዳያነሱ የሪፐብሊካን ሊበርቲ ፓርቲ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ ድጋፍ ሲያሰባስብ ነው የሰነበተው፡፡
የፓርቲው መሪ ቪንሰንት ኪዳላ፤ 1ሺ እርቃን ሴቶችና 4ሺ እርቃን ወንዶች በተቃውሞ ሰልፉ እንደሚሳተፉ አስታውቀው ነበር፡፡ በኦባማ የኬንያ ጉብኝት ዋዜማ ላይ ሊካሄድ ታቅዶ የነበረው የተቃውሞ ሰልፍ፤ ለፕሬዚዳንቱ የወንድና የሴትን ልዩነት ለማሳየት ያለመ ነበር ተብሏል፡፡በመጨረሻው ሰዓት ላይ ግን የእርቃን ተቃውሞው ለጊዜው መሰረዙን የሰልፉ አደራጅ አስታውቋል፡፡ የሪፐብሊካን ሊበርቲ ፓርቲ መሪ ቪንሰንት ኪዳላ፤ ከመንግሥት ቢሮ ስልክ ተደውሎ የእርቃን ተቃውሞ ሰልፉን እንዲሰርዙ መገደዳቸውን ተናግረዋል፡፡
“ስልክ ደዋዩ፤ የኬንያው ፕሬዚዳንት ዩሁሩ ኬንያታ ከባራክ ኦባማ ጋር በግብረ ሰዶማውያን መብት ዙሪያ ለመወያየት እንዳላቀዱና የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻን እንደማይደግፉ ገልጾልኛል” ሲሉ የፓርቲው መሪ ሚዲያ ተናግረዋል፡፡ከብሄራዊ ደህንነት ኮሚቴም ስልክ ተደውሎ፣ የተቃውሞ ሰልፉ እንዳይደረግ ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው ኪዳላ ገልፀዋል፡፡ ማንነቱን ያልገለፀው ደዋይ፤ “የተቃውሞ ሰልፉን ማድረግ የሽብር ጥቃት ከመፈፀም እኩል ነው” ብሎኛል ሲሉ የፓርቲው መሪ አስረድተዋል፡፡
የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻን በመቃወም ሊካሄድ ታስቦ የነበረው ሰልፍ ለጊዜው ይሰረዝ እንጂ ከእነአካቴው እንደማይቀር አዘጋጆቹ አስታውቀዋል፡፡ ፓርቲው በሰጠው መግለጫም፤ ሰልፉ ለሌላ ጊዜ ተላልፏል ነው ያለው፡፡ ጊዜውን ግን አልገለፀም፡፡ ለማንኛውም ኦቦማ አምልጠዋል!!

 “ከልጅ ልጅ ቢለዩ…”
የኦባማ ጉብኝት ኬንያንና ኢትዮጵያን ከምንጊዜውም በላይ ቁጭ ብድግ እንዳሰኛቸው እያየን ነው፡፡ የኬንያ ጋዜጦች እንደዘገቡት፤ ናይሮቢን ጨምሮ ፕሬዚዳንቱ ይጎበኙዋቸዋል የተባሉ ከተሞች ሁሉ ሲታጠቡና ሲቀባቡ ነው የሰነበቱት፡፡ በናይሮቢ ጐዳና የኦባማ ትልቅ ምስል ተሰቅሎ ይታያል፡፡የአሜሪካ የፀጥታና ደህንነት ሃይል ኬንያን የመፈተሽና ከሽብር ጥቃት ነፃ የማድረግ እንቅስቃሴ የጀመረው ከሁለት ሳምንት በፊት ነው፡፡ 8 ሄሊኮፕተሮች ከኦባማ ቀድመው ኬንያ መግባታቸው ይታወቃል፡፡ በነገራችን ላይ… ከተማም… ገፅታም… ፀጥታም ያበላሻሉ ተብለው የታሰቡ… ከ3ሺ በላይ የናይሮቢ የጎዳና ተዳዳሪዎች ተሰብስበው የአንደኛ ደረጃ ት/ቤት ግቢ ውስጥ እንደከተሙ ዘ ስታንዳርድ ጋዜጣ ዘግቧል፡፡ ከጐዳና ተዳዳሪዎቹ ውስጥ ቢያንስ ግማሾቹ ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች ነው ተብሏል፡፡ የማን ሃሳብ ወይም እቅድ እንደሆነ ባይታወቅም ከ3ሺ በላይ እንደሚሆኑ የተገመቱት የጎዳና ተዳዳሪዎች ት/ቤቱ ውስጥ ተከርችመው አይቀመጡም፡፡ ጊዜያዊ የተሃድሶ ማዕከል እንደሚገቡ ተነግሯል፡፡ የናይሮቢ ከተማ ገዢ ኢቫንስ ኪዴሮ ስለ ፕሮጀክቱ ሲናገሩ፤ “የተሃድሶ ፕሮግራሙ የምግብ፣ የልብስና የመጠለያ አቅርቦትን ይጨምራል፡፡ በጐዳና ላይ ከለመዱት የተሻለ ምቾት ያገኛሉ” ብለዋል፡፡ የናይሮቢ ከተማ መስተዳድር ሰዎቹን ከጎዳና ላይ ሰብስቦ ለማንሳት 40ሚ. የኬንያ ሽልንግ መቀበሉን ኪዴሮ ገልፀዋል፡፡ የገንዘቡ ምንጭ ባይጠቀስም ከኦባማ መንግስት ሊሆን እንደሚችል ተገምቷል፡፡ በተሃድሶው ፕሮግራም የጎዳና ተዳዳሪዎቹን ከእነአካቴው ከጐዳና ህይወት የማላቀቅ ዘላቂ ዕቅድ ይኑር አይኑር አልታወቀም፡፡ ቢሆንላቸውማ በማን ዕድላቸው! “የራሷ አሮባት የሰው ታማስላለች…” ብትሉኝ አመሰግናችሁ ነበር፡፡ ለመሆኑ የእኛስ የጐዳና ተዳዳሪዎች የት ገቡ? ኦባማ መቼም አይረሷቸውም ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡ “ከልጅ ልጅ ቢለዩ…” ነው ነገሩ፡፡

   ምንም ነገር የማይሞቀው ምንም ነገር የማይበርደው ሰው መሆን አማረኝ፡፡ ወሬ የሙቀት እና የቅዝቃዜ ምንጭ የሆነበት ማህበረሰብ ውስጥ ሆኜ በሰው ሰራሽ አደጋ እየተጠቃሁ በመቸገሬ ምክንያት ነው፡፡
በወሬ በኩል የፌስ ቡክ ማህበረሰብን የሚያክል የለም፡፡ በወሬ የተገነባ ማህበረሰብ በወሬ ይፈርሳል፡፡ ፌስ ቡክ መተዳደሪያ ደንብ የለውም፡፡ ጓደኝነት በምን ምክንያት እንደተመሰረተ፣ በምን ምክንያት እንደፈረሰ አይታወቅም፡፡
ማንነቱን ለማጣት የማይፈልግ ካለ “stoic” በመሆን ብቻ ነው መትረፍ የሚችለው፡፡ “እስቶይክ” ሆኖ ለመትረፍ ጆሮን በጥጥ ወይንም በዳባ መድፈን ብቻ ነው የሚያዋጣው አማራጭ፡፡ ማንን ታዳምጣለህ? ብትሉኝ “ሁሉንም” ነው መልሴ፡፡ ሁሉንም የሚያዳምጥ ማንንም በቅጡ አይሰማም፡፡ “አይሰማም” የሚለው ቃል ከሰው የማድመጥ ተፈጥሮ ጋር ሳይሆን … ከምጣድ የመጋል ችሎታ ጋር የሚተሳሰር ባህርይ ነው፡፡ ምጣድ በኮሬንቲ እሳት ወይ በማገዶ እሳት ነው የሚሰማው፡፡ ምጣድ እውቀትን ወይንም ምክንያታዊነትን በእሳት መልክ ከተሰጠው ብቻ ይቀበላል፡፡
የፌስቡክ ማህበረሰብ የሚሰማው ጫጫታን ነው፡፡ ጫጫታ “ያሰማዋል”  .. ይሰማዋል፡፡ ጫጫታ ውል የለውም፡፡ እረኛም የሚያግደው አይደለም፡፡ በሆነ ቅፅበት ተሰብስቦ … የነበረበት ቦታ ቅፅበቷ ስታልፍ ተከማችቶ አይገኝም፡፡ ሲሰበሰብ ይንጫጫል … ጫጫታው ድጋፍ ሊመስል ይችላል .. ወይንም ደግሞ ተቃውሞ፡፡ ሊመስል የቻለውን ያህል ሆኖ ያለመገኘት አቅም አለው፡፡
በአንድ ወቅት አንድ ወዳጅ “መፅሐፍትን ለማንበብ የሚያበረታታ ፅሁፍ ፃፍ” ብሎ ወተወተኝ፡፡ ስለ መፅሐፍት መነበብ ከሚገደው በላይ የመፅሀፍት ንባብን አበረታትቶ ወይንም ያበረታታ መስሎ የሚቀበለው ብር እንዳለ አውቄያለሁ፡፡ እኔም ሳይገደኝ እንድፅፍ እሱም ሳይገደው ለማስተዋወቅ ነው ያሰበው፡፡ ሌላ ግድ የሌለው ድርጅት ደግሞ እሱ እና እኔን ይከፍለናል፤ በዚህ ተስማማን፡፡ በዚህ ስምምነት ውስጥ እውነት ከእነ አድራሻዋም የለችም፡፡
አዎ ሲወራ እሰማለሁ፡፡ መፅሐፍ ማንበብ ዋናው ነገር ስለመሆኑ፡፡ “መፅሐፍ” የሚባለው ነገር ምን እንደሆነ በጥንቃቄ መመርመር ሳያስፈልገኝ አይቀርም፡፡ ለመሆኑ ተጨባጭ መፅሐፍ ተብሎ የሚጠራ ነገር አለ? .. ልክ “Virtue” (ሰናይ) እንደሚባለው ፅንሰ ሀሳብ፣ መፅሐፍ የሚባለውም ነገር የሆነ Abstract Concept ስላለመሆኑ ማረጋገጥ አልቻልኩም፡፡ ሰናይነት ወይንም እኩይነት (Vice) በሆነ ተጨባጭ የሰውኛ ማንነት ላይ ተንፀባርቆ እስካላገኘን ድረስ ነገርየው በሰማይ ላይ የተንጠለጠለ ፅንሰ ሀሳብ ነው፡፡
መፅሐፍ ቅዱስ ለምሳሌ፤ ቅዱስነትን ከመፅሐፍ ጋር አጣምሮ ሰማይ ላይ የተንጠለጠለውን ፅንሰ ሀሳብ ወደ ምድራዊ ትርጓሜ የሚያመጣ ነው፡፡ መፅሐፍ ቅዱስ… መፅሐፍ ብቻ ቢሆን ወይንም ቅዱስ ብቻ ቢሆን … የተፈጠረውን፣ የተዋሀደውን ትርጉም አይሰጠንም፡፡ ቅዱስ የሆኑ ምድራዊ ሰዎች በመፅሐፉ አለም ላይ ምን እንደሚመስሉ እናነባለን… ስለ ሰማዩ ሰናይነት በምድራዊ ፊደላት አንብበን የቆምንበትን ከራቀን ቅዱስነት ጋር አመሳክረን እንረዳለን፡፡
“ቅዱስነት” ብቻውን ምድራዊ መወከያ እስካልተቆራኘው ድረስ ተንሳፋፊ ፅንሰ ሀሳብ እንደሆነው “መፅሐፍነትም” ብቻውን ትርጉም የለሽ ነገር ነው፡፡
መፅሐፍነታቸው ከፅንሰ ሀሳብነት ላይ ብቻ ሆነው ህይወቴን በውስጣቸው ማጥመድ ያልቻልኩባቸውን ነገሮች ቤቴ ውስጥ ደርድሬያቸዋለሁ፡፡ ከእነዚህ መፅሀፍ ተብለው ከተሰየሙ ነገሮች ውስጥ አንደኛው ዳጎስ ያለ ገፅ ያለው፣ ጠንካራ ልባስ ወይንም ቅርፊት የተለበጠ .. “የማርክሲስት ሌኒኒስት መዝገበ ቃላት” የሚል የዳቦ ስም የወጣለት ነው፡፡ መፅሀፉን እንደ ጣውላ ቴሌቪዥኔን ለማስቀመጫነት ነው የምገለገልበት፡፡ ከፅንሰ ሀሳባዊ አገልግሎቱ ይበልጥ ተጨባጭ አገልግሎቱ ለእኔ ይጠቅመኛል፡፡
በዚሁ አንፃር መፅሀፍትን መመልከት ጀምሬአለሁ፡፡ ዝም ብሎ “መፅሐፍ” ብሎ ነገር የለም፡፡ የወረቀት ክምችት የተጠረዘበት መፅሐፍ… “የወረቀት ክምችት” ተብሎ ግልፅ ያልሆነ ማንነቱ ወደተገለፀው እና ተጨባጭ ምንነቱ መስተካከል አለበት፡፡ በኬሻ ውስጥ የተጠራቀመ ቁሻሻ … “ቁሻሻ” ተብሎ የተጠራው አስፈላጊነቱ በማለቁ ነው፡፡ የከረሜላ ልጣጭ ለእኔ የማይጠቅመኝ… የከረሜላ ዋናው ትርጉም ጣፋጭነቱ ላይ የሚገኝ በመሆኑ ነው፡፡ ድቡልቡል ባልጩት ብጠቀልልበት ነገርዬው የከረሜላን ትርጉም አይሰጠኝም፡፡
መፅሐፍም በወረቀትነቱ ብቻ ከልጣጭ የበለጠ ትርጉም የለውም፡፡ በፊት ትምህርት ቤት ሳለን የተማርንባቸውን ደብተሮች በኪሎ ለባለ ሱቅ እንሸጥ ነበር፡፡ ትምህርትን በውስጡ የያዘ ደብተር የትምህርቱ ጊዜ ሲያልቅ አስፈላጊነቱም ያበቃል፡፡ አንድ አስፈላጊነት ሲያበቃ ሌላ አስፈላጊነትን ቀድሞ በነበረው ፋንታ ተክቶ ነው፡፡ ከትምህርት ደብተሮቹ ጋር መፅሐፍትም ለኪሎ ገበያ ይቀርባሉ፡፡ ስኳር እና እርድ ይጠቀለልባቸዋል፡፡
መፅሐፍ ስለተጠረዘ ብቻ መፅሀፍ ሆኖ አይቆይም፡፡ እያንዳንዱ መፅሐፍ ከወረቀትነቱ ባሻገር ያለ አንዳች “ምንነቱ” ፅኑ ካልሆነ … በስተመጨረሻ ወረቀቱ ብቻ ይቀራል፡፡ አንዱ አስፈላጊነት utility ወደ ሌላ ይሸጋገራል፡፡ የአበባ ውበቱ ያለው በፍካት ወቅት ነው፡፡ ከጠወለገ በኋላ አበባም ለማገዶ የማይሆን ጭራሮ ነው፡፡
መፅሐፍ ምን ማለት እንደሆነ ለማወቅ ሰው ምን እንደሆነ በቅድሚያ ማወቅ ሳያስፈልግ አይቀርም፡፡ ግን “ሰው” ራሱ አብስትራክት ፅንሰ ሀሳብ ነው፡፡ ድሮ በጥንቃቄ ይያዝ የነበረ ደብተር አሁን ግን በኪሎ የሚሸጥ ደብተር ሆኖ እንደዘቀጠው ሁሉ … ድሮ መሳፍንት ተብሎ ጥሩ ስፍራ ይደረደር የነበረ ሰውነት ማንነቱ በኪሎ ሚዛን እንኳን ትርጉም የማይሰጥ ተራ ይሆናል፡፡
“መፅሐፍነት” ብቻውን ቋሚ ትርጉም እንደሌለው፤ ሰውነትም ብቻውን መለኪያ አይፈጥርም፡፡ ሰው ከሚለው ጎን “ምን አይነት ሰው?” የሚለው (essence) መግለጫ ክፍት ቦታ ትርጉም ግዴታ መሞላት ያስፍልገዋል፡፡ “ምን ዓይነት ሰው” ብቻ ሳይሆን ምን አይነት ሰው በምን አይነት ዘመን? የሚለውንም መመለስ ያሻል፡፡
በዶስቶዮቭስኪ የተደረሰ መፅሐፍ እና የአሜሪካ ዜግነት መታወቂያ ያለው ሰው በአሁኑ ዘመን የመፅሐፍነትን እና የሰውነት ሁነኛ መለኪያ ተደርገው ሊወሰዱ ይችላሉ፡፡ በማርክሲስት መዝገበ ቃላት መፅሐፍ እና በደርግ ዘመን ካድሬ ከነበረ ሰው በወቅታዊው የተፈላጊነት ገበያ ተመን ዋጋ  የሌላቸው ይመስለኛል፡፡ ከመሰለኝ ደግሞ (ብዙ ጊዜ) ነው!
የሰውም ምንነት በተገለባባጭ የርዕዮተ ዓለም ገበያ እና የርዕዮተ አለሙን ሚዛን በሚዘውረው ኢኮኖሚ ሀያልነት ውስጥ ያለ ፅኑ ዋልታ የሚዋዥቅ ነው፡፡ የፈለገ ቢዋዥቅም … በስተመጨረሻ ሰውን ከእንስሳ ዓለም ጋር አንድ የሚያደርገው የተፈጥሮ ልክ ግን ስፍራውን ስቶ አያውቅም፡፡ መፅሐፍም ሲጠቃለል ወረቀት …ሰውም በስተመጨረሻ እንስሳ ነው፡፡
እናም የ“ሰው” ምንነት ፍቺ በሀሊዮት ምክንያት ቢዋዥቅም የተፈጥሮ እንስሳነቱ ግን አስተማማኝ ሆኖ ይቀጥላል፡፡ በዛው አንፃር መፅሐፍም በውስጡ የያዘው “ምንነት” እንደ ገበያ ተፈላጊነቱ ወይንም እንደ ወረትነቱ - ቢለዋወጥም … ዋና የተፈጥሮ ማንነቱ፣ ወረቀትነቱ አስተማማኝ ሆኖ ይዘልቃል፡፡
ከፌስቡክ ማህበረሰብ ተነስቼ ወደ መፅሐፍት የማንነት ዓለም ያሳበርኩት ሰውን እና የመፅሐፍትን ግንኙነት በበለጠ ለመረዳት የሚያስችል ወቅታዊ ማስረጃ ከፌስቡክ ማግኘት ስለሚቻል ነው፡፡ የሰውን ተለዋዋጭ ማንነት ከመፅሐፍት ተለዋዋጭ ትርጉም ጋር ለውሶ ለማጣጣም ከዚህ ማህበረሰብ የበለጠ ማሳያ የሚኖር አይመስለኝም፡፡
መፅሐፍት ከወረቀት በላይ ከሰው በላይ ሊሆኑ ይችላሉ፤ ወይንም ከሰውም ከወረቀትም በታች፡፡ ይሄንን ሊያደርጋቸው የሚችለው ሰው ራሱ ነው፡፡ የሰው የማንነት ትርጉም ከፍ ባለባቸው ዘመኖች የመፅሐፍትም የማንነት ትርጉም ከፍ ይላል፡፡ ሰው የማንነት ትርጉሙን ከፍ የሚያደርገው በእውቀት ብቻ ነው… እውቀት ደግሞ ተጠራቅሞ የሚገኘው በመፅሐፍት ውስጥ ብቻ ነው፡፡ ሰው በትክክለኛው /በሚመጥነው/ የራሱ ማንነት ውስጥ ተጠራቅሞ ሲገኝ በመፅሐፍ ውስጥም የሰው ማንነት ውሎ ይነበባል፡፡
ሰው ከራሱ ማንነት ሲወርድ መፅሐፍትም ሰው በሰየመላቸው የማንነት ትርጉማቸው ይወርዳሉ፡፡ የወረደ መፅሐፍ ወደ ወረቀትነቱ … የወረደ ሰው ወደ እንስሳነቱ ሲያቆለቁሉ መሀል መንገድ ላይ ይገናኛሉ፡፡ የወረደው ሰው የቅኔውን ፅሁፍ ወደ ሽንት ቤት ወረቀትነት ቀይሮ ለወቅታዊ ጥሪው ሊገለገልበት ይችላል፡፡
የመፅሐፍት መብዛትን ከሰው መብዛት ለይቼ አልገነዘበውም፡፡ መፅሐፍት የሚያዝሉት ጭብጥ /እውቀት/ እየጠራ፣ እየነፀረ ከመጣ ሰውም ጥራቱን በሀቀኛ ጎዳና እያጣጣመ መሆኑን ያመለክተኛል፡፡
በተደጋጋሚ ራሴ ስናገር የማደምጠው እና የሚያስቀኝ አባባል አለ፡፡ እኔ ራሴ እየወረድኩ በመምጣቴ ምክንያት መሆን አለበት ድሮ እንደ መመሪያ አምንበት የነበረው ነገር ዛሬ ሳላምንበት እንደው ከንፈር ለማልፋት ብቻ ስደጋግመው በውስጤ የሚያስቀኝ፡፡
“በመፅሐፍት መደርደሪያዬ ላይ ሀምሳ ምርጥ መፅሐፍት እንዲኖሩኝ ነው የምፈልገው” እላለሁ፡፡ “ሀምሳዎቹ መፅሐፍት የምድርን እውቀት በኦርጅናልነት ያበረከቱት መሆን አለባቸው፡፡ ከእነዚህ መፅሐፍት ውስጥ ነው ሌሎቹ እንደ አፈር የፈሉት የሰው ልጅ ድርሰቶች የተገኙት፡፡ እነዚህን ሀምሳ መፅሀፍት ከተቆጣጠርኩ፣ አለሙን እና የራሴን ማንነት በራሴ እጅ በህይወት ዘመኔ ውስጥ አንፀዋለሁ”
እነዚህ ሀምሳ መፅሃፍት የትኞቹ እንደሆኑ አላወቅሁኝም፡፡ ከሀምሳዎቹ መሀል ሊጠቀሱ ይችላሉ ብዬ የምጠረጥራቸው አሉ፡፡ ግን በስተመጨረሻ ምን ዋጋ አለው … መፅሐፍቱን ሳገኝ እኔ ራሴን ማግኘት አቅቶኝ ከሆነ!
እኔና የዓለም ህዝብ አንድ ላይ ግልብ ከሆንን ምን ዋጋ አለው? መፅሐፍቱ በሰው ተፅፈው እኛ ዘመን ላይ ሲደርሱ የወፍ ቋንቋ ከሆኑብን፣ አጥረን የአባቶቻችን የስልጣኔ ሱሪ ከረዘመን፣ እንደ አረጀ አንበሳ የጫጫታ ዝንብ ከወረረን፣ በወጣትነታችን እውቀትን ለመቀበል እና ለማሸጋገር ሳንችል ካረጀን? … ምን ዋጋ አለው?
T.5 Eliot “I grow old, I grow old / I wear the bottom of my trousers rolled” ያለው ይሄንን ከሰውነት “ቁመና” መዝቀጥ፣ ማጠር አጢኖ ሳይሆን አይቀርም፡፡
መፅሐፍትን ለማንበብ መጀመሪያ ማንበብ መቻል ይቀድማል፡፡ መፅሐፍን መፃፍ ደግሞ ሁለት እጥፍ ይቀድማል፡፡ በአጭሩ ስለ መፅሐፍት ሚዛናችን አብዝተን ማሰብ ይኖርብናል፡፡

Published in ህብረተሰብ
Monday, 27 July 2015 10:27

አቤቱታ ለአንድዬ…

 እንዴት ሰነበታችሁሳ!
መስከረምም ደረሰ፣ ሌላ ዓመትም ሽው ብሎ ሄደ፡፡ ይኸው ሆኗል ነገራችን-- አሮጌ ዓመት መሸኘት አዲስ ዓመት መቀበል፡፡ አምና ከዘንድሮው እየተሻለ ከተረተ አያልፍም ያልነው ነገር ሁሉ እውነት እየሆነ ይኸው እዚህ ደረስን፡፡
ምስኪን ሀበሻ:- አንድዬ ከብዙ ጊዜ በፊት እንዲሁ ነገሩ ሁሉ ግራ ቢገባኝ አዋይቼህ ነበር፡፡ አስታወስከኝ?
አንድዬ:- ማን ልበል አንተን?
ምስኪን ሀበሻ:- ይሄን ያህል ረስተኸኛል ማለት ነው? የሰው ልጅ መገኛ፣ የስልጣኔ መሠረት አገር ይዤ ምን ልበል ትለኛለህ? እሺ ይሁን… ምስኪኑ ሀበሻ፡
አንድዬ:- ይቅርታ… ምስኪን ሀበሻ ልጅ ነው ያልከኝ…ዘነጋሁ ልበል!
ምስኪን ሀበሻ:- እንዴት አንድዬ ይኸው ስንት ክፍለ ዘመን ሙሉ እጆቻችንን  ወዳንተ እንደዘረጋን አይደል! እንደው ተሳስተህ እንኳን “እነኛ እጆቻቸውን ያንከረፈፉት እነማን ናቸው ሳትል ቀርተህ ነው?
አንድዬ:- እህ! አስታወስኩ…እኔ የምለው እንደው ክንዳችሁ አለመዛሉ ግርም ይለኛል! የእናንተ ነገር እኮ እኔንም ግራ ገባኝ!
ምስኪን ሀበሻ:- ኧረ አንድዬ ግራ የገባን እኛ ነን። እንዴት ግራ እንደገባን ብታየን በሆነ ተአምር ግራ መጋባትን ከዓለም የሚያጠፋ የሙሴ በትር ትልክልን ነበር፡፡
አንድዬ:- ስማኝ ምስኪኑ ሀበሻ…መጀመሪያ የፈጠርኩት አዳምን ነበር፡፡ የእሱ ዝርያዎች ደግሞ አያሳስቱኝም፡፡ እናንተን ሳያችሁ ከዓዳም ሌላ የሆነ ሰው ፈጥሬ ይሆን እንዴ እያልኩ እራሴን እጠይቃለሁ፡፡ ብቻ ለጊዜው ብዙ ሌሎች የማያቸው ፋይሎች ስላሉ ትኩረቴ ሁሉ ወደዛ ነው፡፡ ትንሽ ተንፈስ ስል ወደ እናንተ እዞራለሁ፡፡
ምስኪን ሀበሻ:- አንድዬ ኧረ ተው ከእኛ የሚብስ የለም! ስንት ስምንተኛው ሺህ መሰለህ አጠገባችን እየደረሰ እያሳዘንነው ነው መሰለኝ ያልፈናል፡፡ አንድዬ ቢያንስ፣ ቢያንስ እንደው ስምንተኛው ሺህ የሚያስመስሉ ነገሮችን ሰውርልን! አንድዬ…እኛስ እንደው እንደሌላው ትንሽ ዘመን እንኳን ሳንቆራቆስ፣ “ግነን በሉኝ” ሳንባባል፣ እርስ በእርስ ሳንጠፋፋ፣ አንዳችን ለሌላችን ጉድጓድ ሳንማማስ… መኖር አያምረንም!
አንድዬ:- እንደሱ ብዬማ ብዙ ሞከረኩ፣ ባያችሁ፣ ባያችሁ እንኳን የራሳችሁን ሰባራ ልትጠግኑ ጭርሱን ወደ እኔ ዞራችሁ፡፡
ምስኪን ሀበሻ:- ኧረ ተው አንድዬ…ምን ብለን ነው ወዳንተ የምንዞረው ማን አለንና! ጠላቶቻችን የሚነዝቱንማ አትስማ፡፡
አንድዬ:- እኔ እኮ የምለው…መቼ ነው ጠላታችን፣ ጠላታችን ማለት የሚበቃችሁ! እንደው በገዛ ፍጡርህ ላይ ጨከንክ አትበለኝና አሁን እኮ የራሳችሁ ጠላት ራሳችሁ ናችሁ፡፡
ምስኪን ሀበሻ:- ጌታዬ፣ አታምርር እንጂ…
አንድዬ:- ደግሞ እኮ የክፋታችሁ ክፋት በገዛ ቤቴ መጥታችሁ የምትጠይቁኝ ጥያቄ የሰይጣን ጆሮ አይስማው እንጂ አንዳንዴ ምን ስል ነው የፈጠርኳቸው እላለሁ፡፡
ምስኪን ሀበሻ:- ምን አደረግን?
አንድዬ:- ቤቴ መጥታችሁ ጤና ስጠን፣ ፍቅር ስጠን፣ ሀብት ስጠን ብትሉ ይገባኛል። ልዩነትን አርቀህ ነፋስ የማይገባው ወንድማማችነትና እህትማማችነት ስጠን ብትሉኝ፣ ምንም እንኳን ለእኔም እንኳን የሚያስቸግር ቢመስልም፣ ይገባኛል፡፡
ምስኪን ሀበሻ:- አፋቅረንና አዋደን ከማለት ሌላ ምን አልን! እንደ ባህር አሸዋ ሀብት አብዛልን ከማለት በስተቀር ምን አልን!
አንድዬ:- ‘የእሷን ነገርማ ካላሳየኸኝ፣’ ‘እሱን ልክ ካላገባህልኝ’ እያላችሁ ጭርሱን…የዲያብሎስን ሥራ ወደ እኔ ታዞሩ፡፡
ምስኪን ሀበሻ:- አንድዬ ቢጨንቀን እኮ ነው…ሰዉ አላስቀምጠን ቢለን እኮ ነው! ጉልበተኛ እየበዛብን አቅም ቢያንሰን እኮ ነው!
አንድዬ:- ደግሞም ቤቴን ተሳልማችሁ ትወጡና በሩን በሚገባ ሳትሻገሩና የጸሎት መጽሐፍ ከኪሳችሁ ሳይወጣ ጠጠር ብተና ትሄዳላችሁ…ኧረ
ምስኪን ሀበሻ:- አንድዬ…ጨነቀና! አንተ ዝም ስትለን ሌላ በኩል እንሞክር ብለን ነዋ! ጌታዬ የቸገረው እርጉዝ ያገባል እያልን ስንተርት አልሰማህም! እዚህ፣ እዛ የምንለው ከጭንቀት ነው፡፡
አንድዬ:- ዶሮውንና ንፍሮውን በየሰዉ አጥር እየጣላችሁና እየበተናችሁ ምግብ አጠረን፣ ራበን ትሉኛላችሁ፡፡ ጽላቱን ምኑን ምናምኑን እየጫናችሁ እየወሰዳችሁ… ተወው እባክህ፣ አድሮ ጭቃ ለሚሆን ነገር ትንፋሼን የምጨርሰው እንዲሁ ነው፡፡
ምስኪን ሀበሻ:- አንድዬ አታምርር እንጂ…
አንድዬ:- አሁን ዋናው ነገር ለምን ነበር ፈለግሁህ ያልከኝ?
ምስኪን ሀበሻ:- ኧረ አንድዬ እኛ እኮ ሁልጊዜ እንደፈለግንህ ነው፡፡
አንድዬ:- ቤቴ መጥታችሁ ጽላትና መስቀል ሸጉጣችሁ የምትወጡ ጉዶች… በአፋችሁ እኔን እያመሰገናችሁ በልባችሁ ሉሲፈርን የምትለማመኑ…አሁን እኔን የምትፈልጉኝ ክፋታችሁን፣ ሀጢአታችሁን እንድባርክላችሁ ነው!
ምስኪን ሀበሻ:- አንድዬ አንዳንድ ምግባረ ብልሹዎች እኮ በየቦታው አይጠፉም…ሁላችንንም አትውቀሰና!
አንድዬ:- ትሰማኛለህ የእኔን ቃል የሚያስፋፉ እኮ በባዶ እግራቸው እሾሁና ቆንጥሩ እየወጋቸው፣ ጦማቸውን እየዋሉ እያደሩ፣ በየበረሀው እየተንከራተቱ ነበር፡፡ አሁን የመኪና አይነት እያማረጥክ፡ በፎቅ ላይ ፎቅ እየከመርክ የመልካም ምግባርና የሀጢአትን ትርፍና ኪሳራ ከማስላት ይልቅ በሰበብ አስባቡ በእምነት ስም የምትሸጠውን ቁሳቁስ ትርፍና ኪሳራ እያሰላህ አንድዬ፣ አንድዬ እያልክ ልትባባልኝ አትሞክር፡፡
ምስኪን ሀበሻ:- ዛሬ የእውነትም ተበሳጭተህብናል ማለት ነው…
አንድዬ:- በቪላ ቤት እየተንደላቃቃችሁ፣ በዘመናዊ መኪና እየተንደላቀቃችሁ፣ ቀን የለበሳችሁትን ልበሰ ተክህኖ ሌሊት በብጣሽ ጨርቅ የምትለውጡ፣ በእኔ ስም የቀረቧችሁን እሀቶቻችሁን ለተራክቦ ስታግባቡ..
ምስኪን ሀበሻ:- ኧረ አንድዬ ሀጢአታችንን እንዲህ አታብዛብን! ምግባረ ብልሹዎች በየቦታው አሉ እያልኩ እኮ ነው፣ አንድዬ!  ታዲያ በጥቂት ምግባረ ብልሹዎች ሁሉም አይኮነንማ!
አንድዬ:- እኔም ሁሉንም አልኮነንኩም፡፡ አሁንም ልበ ንጹሀን፣ ምግባረ ሰናዮች ሞልተዋል፡፡
    ግን ትሰማኛለህ፣ ምስኪን ሀበሻ… ማን ምን እንደሚሠራ እያንዳንድህ ታውቀዋለህ። ደግሞ እኮ የሁልህም መጀመሪያ አንድ ዓዳም ያልነበረ ይመስል… ሦስት አራት ቦታ ጎጥ እየለያችሁ የወንዜ ልጅ፣ የአገሬ ልጅ እየተባባላችሁ ስሜን የማትፈልጉትን ማጥቂያ፣ የምትፈልጉትን መጥቀሚያ እያደረጋችሁት ነው፡፡
ምስኪን ሀበሻ:- ምን መሰለህ አንድዬ ትምህርቱ እየተበረዘ…
አንድዬ:- ጠባያችን እየተበረዘ በለኝ እንጂ፡፡ ቀን በእኔ ስም ዘምራችሁ ማታ እርቃናችሁን አሼሼ ገዳሜ የምትሉ..
ምስኪን ሀበሻ:- አንድዬ፣ አሁን ምን መሰለህ፡፡ ግራ ገባን፣ ተደነጋገረን…ብቻ ምን አለፋህ ሀበሻ ለሀበሻ እንዲሁ በነገር ተባልተን ልንተላለቅልህ ነው፡፡ መተማመን ጠፋ፣ ወዳጅነት ጠፋ፡፡
አንድዬ:- እኮ ምን አድርግ ነው የምትለኝ?
ምስኪን ሀበሻ:- ተአምሩን ላክልና አንድዬ! ተአምሩን ላክልን፡፡ የሚያስተቃቅፈንን፣ የሚያዋድደንን ተአምሩን ላክልን!
አንድዬ:- ከራሴ ጋር ልምከርና እነግርሀለሁ፡፡
ምስኪን ሀበሻ:- አንድዬ አንተም እንደ እኛ ቀጠሮ!
አንድዬ:- አዎ ቀጠሮ…ምን መሰለህ፣ የሀበሻ ልጅ… እንዳንተ በየጊዜው በሬን እያንኳኩ የማይጨቀጨቁኝ፣ ሥራቸውን እየሠሩ አበርታን የሚሉኝ፣ ንፍሮን ለምግብነት የሚጠቀሙ እንጂ በየሜዳው በትነው ራበን የማይሉ…  ብዙ ስላሉ ሰሞኑን እነሱን እንዴት እንደምሸልም እያሰብኩ ስለሆነ የአንተን ጉዳይ በኋላ እመለስበታለሁ፡
ምስኪን ሀበሻ:- አንድዬ!
አንድዬ:- ጨረስኩ፡፡
የእነሱን ጉዳይ ቶሎ ጨርሶ ሃሳቡን ወደ እኛ የሚያዞርበትን ጊዜ ያፍጥልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል
Page 3 of 17