አዲሱ የተጨዋቾች ደረጃና የዝውውር መመሪያ ባለድርሻ አካላትን ሳያስማማ ተግባራዊ መሆን ጀምሯል፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን አፅድቄዋለሁ የሚለውን ይህ መመርያ ከሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ሕጋዊ ሰነድ ሆኖ እንደሚቀጥል ገልፆ እየሰራበት ነው።  ከመመርያው ተግባራዊነት በፊት ተጨማሪ ውይይት እንደሚያስፈልግ የተጨዋቾች ተወካዮች  በደብዳቤ ቢጠይቁም ምላሽ አልተሰጣቸውም፡፡ ለፕሪሚዬር ሊግ  ክለቦችም የመመርያው አፈፃፀም በቀጣዩ የውድድር ዘመን በሚኖራቸው ዝግጅት  ላይ እንቅፋት እየሆነባቸውም ይገኛል፡፡
መመርያው ተግባራዊ ከመሆኑ 1  ሳምንት ቀደም ብሎ በክለቦች መካከል የተፈጠሩ ውዝግቦች ነበሩ፡፡ ይህን ተከትሎ የፌዴሬሽኑ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት በመመርያው ቀጣይ ዕጣ ፈንታ ላይ ለመነጋገር ስብሰባ ቢቀመጡም ሳይስማሙ እንደተለያዩ ተነግሯል፡፡
መመርያው ተጨዋቾችንና ቀጣሪዎቻችንን በዋናነት ይመለከታል በማለት የተጨዋቾች ማህበር ተወካዮች ያቀረቡት  ግልፅ ደብዳቤ ትኩረት ስለተነፈገው  ቅር ተሰኝተዋል፡፡  ተጨዋቾቹ በመመርያው የሚመክሩበት ጊዜ እንዲሰጣቸው ፣ በአገሪቱ የአሠሪና ሠራተኛ ውል መሠረት በሁለት ባለጉዳዮች መካከል በሚደረገው ስምምነት ሦስተኛ ወገን እንደማያስፈልግ፣ የክፍያውን መጠንና የአከፋፈሉ ሒደትን በተመለከተም በሁለቱ ባለጉዳዮች ስምምነት የሚወሰን እንጂ በሦስተኛ ወገን ወይም ፌዴሬሽን ሊሆን እንደማይገባ በመጠቃቀስ መስተካከል ስላለባቸው አንቀፆች እንነጋገር ብለው ነበር።   በተለይ ሰኔ 30 ከሆነ በኋላ በሁሉም የፕሪሚዬር ሊግ ተወዳዳሪ ክለቦች    ብዙ ተጨዋቾች ኮንትራታቸው ስለተጠናቀቀ ክፍት በሆነው የዝውውር ገበያ ውላቸውን ለማደስም ሆነ ክለብ ለመቀየር  በፊርማ ክፍያ በተፈጠሩ አለመግባባቶች እየተስተጓጎለ ይገኛል፡
በተለይ በመመርያው እያንዳንዱ ክለብ በስብስቡ ሊኖረው የሚገባን የውጭ ተጫዋቾችን በተመለከተ ቁጥሩ ከአምስት ወደ ሦስት ዝቅ እንዲል መባሉ እና የፊርማ ክፍያ የሚለው አሰራር ተቀይሮ ተጨዋቾች በደሞዝ አገልግሎት እንዲሰጡ በመመርያው መደንገጉ በቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብና በተጨዋቾች ማህበር ተቀባይነት አልነበራቸውም፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ የውጭ ተጨዋቾችን ለመገደብ ደንብ ያስፈለገው ለአገር ውስጥ እግር ኳስ ተጫዋቾች የተሻለ ትኩረት መስጠት ያስችላል ብሏል፡፡  የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ሃላፊዎች በበኩላቸው የውጪ አገር ተጫዋቾች ወደ ኢትዮጵያ መምጣት ያሉትን ጠቀሜታዎች በመዘርዘር ለማስረዳት ሙከራ አድርገዋል፡፡ የውጭ አገር ተጨዋቾች በክለብ ስብስብ መካተታቸው የአገር ውስጥ ተጨዋቾችን በተፎካካሪነት ጎልተው እንዲወጡ እንደሚያደርግና የፕሮፌሽናልነት ዕድል እንዲፈጠርላቸው ያደርጋል የሚሉ ማስረጃዎችንም ገልፀዋል፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን በኢትዮጵያ ለመጫወት ከአፍሪካ 6 አገራት የተውጣጡ ከ26 በላይ ተጨዋቾች በ7 ክለቦች በመቀጠር ህጋዊ እውቅና በማግኘት ለመጫወት ችለው ነበር፡፡ የውድድር ዘመኑ ከመጀመሩ በፊት የእግር ኳስ ፌደሬሽን ይፋ አድርጎት በነበረው ዝርዝር መሰረት በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ሲጫወቱ የነበሩት 26 የሌላ አገር ተጨዋቾች 8 ከካሜሮን፤ 7 ከናይጄርያ፤ 6 ከጋና፤ 3 ከኡጋንዳ እንዲሁም ከኬንያ እና ከደቡብ አፍሪካ የመጡ ናቸው፡፡ ከ26ቱ የሌላ አገር ተጨዋቾች ጊዮርጊስ 7፤ ኤልፓ እና ሀረር ቢራ እያንዳንዳቸው 5፤ ደደቢት 4፤ ኢትዮጵያ ቡና እና ድሬዳዋ ከነማ እያንዳንዳቸው 2 እንዲሁም ኒያላ ለ1 ተጨዋች ቅጥር ፈፅመው በፌደሬሽኑ የእውቅና ማረጋገጫ የውድድር ዘመኑን አሳልፈዋል፡፡
በኢትዮጵያ እግር ኳስ የተጨዋቾች ዝውውር ገበያ እየተሟሟቀ የመጣው በተለይ ካለፉት አራት ዓመታት ወዲህ ነው፡፡ በተለይ የፊርማ ክፍያ ከተባለው አሰራር ጋር ተጨዋቾች ከፍተኛ ጥቅም እያገኙ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ የዝውውር ገበያ ካለፈው 4 ዓመት ወዲህ በ50ሺ ብር የፊርማ ክፍያ ተጀምሮ፤ ወደ 100ሺ ብር ከዚያም ወደ 200ሺ ብር፤ 300ሺብር በአማካይ ወደ 500 ሺ ብር ደርሷል፡፡
የተጨዋቾች ደረጃና የዝውውር መመርያ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ባቀረበው ጥያቄ በተለይም የመመርያው ዋና ተዋንያን ተብለው በሚጠቀሱት ተጨዋቾች ባቀረቡት ግልፅ ደብዳቤ ሳይፀድቅ ለውይይት በድጋሚ ይቀርባል የሚለው ተስፋ ባለመሳካቱ  ሁኔታዎች የተድበሰበሱ መስሏል፡፡   የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ይፋ ባደረገው መግለጫ ከሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም የመመሪያው ተግባራዊነት እንደሚጀመር አረጋግጦ፤ መመሪያው እንደተሻሻለ ወይም ተግባራዊ እንደማይሆን ከአንዳንድ ወገኖች እየተሠነዘረ የሚገኘው አስተያየት መሠረተ ቢስ ብሎታል፡፡ በመመርያው  የአፈጻጸም ሂደት የሚያጋጥሙ ችግሮችን መሰረት በማድረግ በየጊዜው በሚደረግ ፍተሻ የማሻሻያ እርምጃዎች እንደሚወሰድ የፌዴሬሽኑ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አቋም መሆኑን ያመለከተው የፌደሬሽኑ መግለጫ፤  በቀጣይነትም መመሪያውን በተመለከተ ከተለያዩ አካላት የሚቀርቡትን ገንቢ አስተያየቶች ፌዴሬሽኑ እየተቀበለና እያጤነ በማሻሻል አስፈላጊውን መግለጫ የሚሰጥ መሆኑ እንዲታወቅ መመሪያውን በተመለከተ የተለወጠ ወይም የተሻሻለ ሁኔታ ባለመኖሩ ተግባራዊነቱ የሚቀጥል መሆኑን አሳስቧል፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን  በአገሪቱ የሚፈፀመው የእግር ኳስ ተጨዋቾች ደረጃና ዝውውር በሕግና በሥርዓት እንዲመራ ባለው ፍላጎት መፅናቱን አረጋግጧል፡፡ መመርያው በፊፋ ዝቅተኛውን የተጨዋቾች ደረጃና ዝውውር መስፈርት ያሟላ እንዲሆን፣ በተጨማሪም አሠራሩ በሕጋዊ ወኪል እንዲመራና ሒደቱም ተጨዋቾችን፣ ክለቦችንና መንግሥትን ተጠቃሚ በማድረግ ለአገሪቱ የእግር ኳስ ዕድገት መፋጠን የራሱን አወንታዊ ሚና እንዲጫወት ይፈለጋልም ተብሏል፡፡
በኢትዮጵያ ከተጨዋቾች ዝውውር ጋር ተያይዞ እየተሠራበት የነበረው አሠራር ለአገሪቱ እግር ኳስም ሆነ ለክለቦች፣ ተጨዋቾችና መንግሥት ምንም ዓይነት ጥቅም እንዳላስገኘ የሚገልፀው ፌደሬሽኑ፤ የዝውውር ሂደቱ የክለቦችን የፋይናንስ አቅም ማዳከሙን፤ ለተጨዋቾችም እንደተከፈለ የሚነገረው ገንዘብ ሙሉ በሙሉ እንደማይደርሳቸው፤ ህገወጥ የዝውውር ደላሎች እንደበዙበት፤  በፕሮፌሽናል ስም የሚመጡት ብዙዎቹ ተጨዋቾች የችሎታቸው ጉዳይ ጥያቄ እንደሚያስነሳ፤ ተጨዋቾች ከደመወዝ ይልቅ ትኩረት ሰጥተው የሚከራከሩት ለፊርማ ተብሎ ስለሚሰጣቸው ገንዘብ መሆኑ፣ ገንዘቡን ከወሰዱ በኋላ ለክለባቸው ተገቢውን አገልግሎት እንደማይሰጡ፣  ክለቦች ታዳጊዎችን አሳድገው ማግኘት የሚገባቸውን ጥቅም በማሳጣቱ፣ አዲሱ ደንብ ተግባራዊ መሆኑ ይህን እነዚህን ችግሮች ለማስተካከል መፍትሄ እንደሚያመጣ በዝርዝር አብራርቷል፡፡

    በረመዳን ወቅት የነበሩትን የነብዩ ሙሐመድ ተግባሮች ምን እንደሚመስሉ ብንገምት ምን አልባት ከባድ አድርገናቸው ሊሆን ይችላል፡፡ እውነት የነብዩ የረመዳን ተግባሮች ከባድ ነበሩ?
አምላክ ነብያትን ከራሳቸው ህዝብ መካከል መርጦ ሲልክ÷ህዝቦችን ወደ ትክክለኛው መንገድ እንዲያስገቡና የአምላክ ተገዢዎች እንዲያደርጓቸው በሚል ነው፡፡ ነብያቶች እንደ ሁላችንም ሰዎች ናቸው፡፡ ራእይ መቀበላቸው ወይም በነሱ እና በአምላክ መካከል አንድ ቅዱስ መንፈስ መኖሩ ከኛ የተለዩ ያደርጋቸዋል። ከአምላክ የተቀበሉት ራእይ (ህጐች)፤ በሰው አቅም የሚቻል መሆኑን ለማስተማር፣ በተግባር አሳይተው ለኛ አርአያነታቸውን ያረጋግጣሉ፡፡
ነብዩ ሙሐመድ ልክ እንደ ማንኛውም ሰው ይበላሉ፣ ይተኛሉ፣ ሚስት አግብተው ወልደዋል፣ ማንም የሚያደርገውን ያደርጋሉ፡፡ ነገር ግን የሰው ልጆች አርአያ መሆናቸውንም አሳይተዋል፡፡ ነብዩ አርአያነታቸውን ሲያሳዩ ከተሰጣቸው መመሪያ ውጭ ሆነው አይደለም። የአምላክን ራእይ በተግባር ማሳየታቸው፤ የአምላክ መመሪያዎች በሰው ልጅ አቅም መከወን እንደሚችሉ ለመጠቆም ነው፡፡
ነብዩ ተግባር ላይ አውለው ካሳዩን የአምላክ ትሩፋቶች መካከል አንዱ የረመዳን ፆም ነው፡፡ አማኞች በረመዳን ወቅት የነበረውን የነብዩ የህይወት እንቅስቃሴዎች የመከተል ግዴታ አለባቸው፡፡ ነብዩ በሚስታቸው አኢሻ “የሚራመድ ቁርአን”  መባላቸው አጠቃላይ ህይወታቸው የቁርአን ትርጓሜ በመሆኑ ነው፡፡
ፆም በአማኞች ላይ ግዴታ መሆኑን አምላክ በቁርአን ውስጥ እንዲህ ይገልፀዋል፡-  
“እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ፆም በነዚያ ከናንተ በፊት በነበሩት ህዝቦች ላይ እንደተፃፈው ሁሉ፣ በናንተም ላይ ተፃፈ (ተደነገገ)፣ ልትጠነቀቁ ይከጀላልና (መልካም እንድትሆኑ ለማድረግ)፡፡”
(አል - በቀራ፣183)
በተቀደሰው የረመዳን ወር ላይ የአምላክ በረከቶች የተትረፈረፉ ናቸው፡፡ ነብዩ መሐመድ እንዲህ ይሉናል፡-
“የረመዳን ወር ሲጀምር የገነት በሮች ይከፈታሉ፤ የሲኦል በሮች ይዘጋሉ፡፡ እንዲሁም ሰይጣኖች ይታሰራሉ።”
እንደ እስልምና ጠበብቶች ከሆነ፣ እኛ ሰዎች ደካማ ፍጡር በመሆናችን ለአለማዊ ጥቅም፣ ሐብት፣ ውድድር፣ አሉባልታዎችና ለሌሎች ፈተናዎች ቶሎ እንሸነፋለን፡፡ ነገር ግን የረመዳን ወርን በአግባቡ በመፆምና በመተግበር ተሸናፊ ስሜታችንን እስከወዲያኛው ማሸነፍ እንችላለን ይላሉ፡፡ ለመሆኑ ነብዩ ሙሐመድ በረመዳን ወቅት የነበራቸው ህይወት ምን ይመስላል? የሚከተለውን እንመልከት፡፡
ስግደትና ፍጥሪያ በረመዳን
ለሊቱ ከመንጋቱ በፊት ነብዩ ፆማቸውን ያስራሉ (ይበላሉ)፡፡ ነብዩ የምግብ እጥረት ባለበት ወቅት ቀርቶ የተትረፈረፈ ሲገኝ እንኳን የሚበሉት በጥቂቱ ነው፡፡ የጨጓራችን 1/3ኛ ለምግብ፣ 1/3ኛ ለውሐ፣ ሌላው 1/3ኛ ለአየር መዋል አለበት ብለዋል፡፡ የነብዩን የእግር ኮቴ እንደመከተላችን መጠን፣ በረመዳን የምናግበሰብሰውን ብዙ ምግብ ቀንሰን ምንም ለሌላቸው ምስኪኖች ማካፈል እንዳለብን እስልምና ይመክራል፡፡
ነብዩ የፈጅር (ጐህ ሊቀድ ሲል) ሶላት ከሰገዱ በኋላ አይተኙም፡፡ ከሶላታቸው በኋላ ዚክር (አምላክን ማስታወስ) የማድረግ ልምድ ነበራቸው፡፡ በተጨማሪም ቁርአንን ያነበንቡ ነበር፡፡ ቤተሰቦቻቸው በዚህ ተግባር ላይ አብረዋቸው እንዲሳተፉ ያደርጉም ነበር፡፡ ሙስሊሞች 30 ቀን በሚውለው የረመዳን ወር ላይ፣ 30 ጁዝ ያለውን ቁርአንን፣ በቀን አንድ ጁዝ በመቅራት እንዲያጠናቅቁ ይመከራል፡፡ ነብዩ በኢማም አህመድ ሐዲስ ውስጥ እንዲህ ብለዋል፡-
“ፆምና ቁርአን በፍርድ ቀን ከአላህ ጋር የሚያማልዱን ናቸው፡፡ ፆማችን “ጌታ ሆይ! ይህን ሰው ከምግብና ከሌሎች ፍላጐቶች አቅቤዋለሁ፡፡ እባክህን አማላጅ ልሁንለት?” በማለት አላህን ይጣራል፡፡ ያነበብነው ቁርአን ደግሞ “ይህን ሰው ማታ ከመተኛት ከልክዬዋለሁና እባክህን ላማልደው?” ይልልናል፡፡ የሁለቱም ጥያቄ በአላህ ዘንድ ተቀባይነት ያገኛል”
ጧት ፀሐይ ከወጣች በኋላ አማኞች ግዴታ ያልሆኑ (ሱና) ሁለት የፀሎት (ዱአ) ስግደቶችን አድርሰው ወደ እለት ስራቸው፣ ወደ ት/ቤት ወይም ወደ ቤት ስራቸው መሰማራት እንዳለባቸው የነብዩ ተግባሮች ይመሰክራሉ። ባጠቃላይ በረመዳን ወር የነበረው የነብዩ ህይወት በሶላቶች የተሞሉ መሆናቸውን ሐዲሶች ይናገራሉ፡፡
በረመዳን ወር የማፍጠር (ፆም የመስበር) ጉዳይ ትልቁን ቦታ ይይዛል፡፡ ነብዩ ቀኑን ሙሉ ጾመው አንዳንድ ጊዜ የሚያፈጥሩት በአንድ ቴምር ብቻ ሊሆን ይችላል፡፡ በእርግጥ በርሳቸው ጊዜ ምግብ እንደ ልብ ስለሌለ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን አልፎ አልፎ ብዙ ምግብ ሲያገኙ እንኳን ከላይ የጠቀስነውን 1/3ኛ ብቻ ነበር ወደ ሆዳቸው የሚያስገቡት፡፡ ሐኪሞች ቀኑን ሙሉ የፆመ አንጀት ብዙ ምግብ ከወሰደ የአንድ ሰው ጤና እንደሚታወክ ከነገሩን በተጨማሪ፣ ምግብ ማግበስበስ ከነብዩ የህይወት ፈለግ ጋር የሚጣረስ ነው፡፡
ፀሐይ ጠልቃ ፆማችንን ከሰበርን (ካፈጠርን) በኋላ ተራዊህ የተባለ መስጂድ ውስጥ በጋራ የሚሰገድ ሶላት አለ፡፡ ተራዊህ 23 ረከአ ያሉት የሱና (የፍቃደኝነት) ሶላት ነው፡፡ በተራዊህ ሶላት ሙስሊሞች በአንድ መስጂድ ውስጥ ከመሰባሰባቸው በላይ፣ አንድ ሰው ከአምላክ ጋር ያለውን ግንኙነት በእጅጉ የሚያጠናክርበት ነው፡፡
ምፅዋት በረመዳን
ነብዩ ሙሐመድ በረመዳን ወር በጣም ለጋስ ናቸው። በቡካሪ ሐዲስ ውስጥ ኢብን አባስ እንደዘገቡት፡- “ነብዩ ካለነው ሰዎች መካከል በጣም ለጋስ ናቸው፡፡ በተለይ ደግሞ በረመዳን ወር የበለጠ ለጋስ ነበሩ…”
በተጨማሪ በቡካሪ ሐዲስ ውስጥ ያለው የነብዩ ንግግር ይህን ይመስላል፡-
“በየቀኑ ፀሐይ ስትወጣ በማንኛውም ሰው መገጣጠሚያ ወይም አጥንት (እጅና እግሩ ላይ)” ሰደቃ (ምፅዋት) አለ፡፡ ሁለት ሰዎችን በፍትሐዊነት መዳኘት ሰደቃ (ምፅዋት) ነው፡፡ አንድን ሰው በመጓጓዣ እንስሳው ላይ እንዲወጣ ማገዝ ወይም እቃውን መጫን ሰደቃ ነው። መልካም ንግግር ሰደቃ ነው፡፡ ለስግደት የምናደርገው እያንዳንዱ እርምጃ ሰደቃ ነው፡፡ ከመንገድ ላይ እንቅፋቶችን ማስወገድ ሰደቃ ነው፡፡” በሌላ ሐዲስ ላይ ደግሞ “ፈገግታ በራሱ ሰደቃ ነው” ብለዋል፡፡
ምስጋና በረመዳን
አማኞች ሁልጊዜም ቢሆን አመስጋኞች መሆን አለባቸው፡፡ በተለይ ደግሞ በረመዳን ወር የምስጋናቸው መጠን ከፍ ማለት አለበት፡፡ በአል-አልባኒ ሐዲስ ውስጥ ነብዩ ይህን ተናግረዋል፡-
“በእርግጥም ምግብ የበላና ውሐ የጠጣ አንድ ሰው፣ ለአላህ የሚያቀርበው ምስጋና ከፆመኛ ሰው እኩል ምንዳ ያስገኝለታል፡፡”
አላህ በቁርአን ውስጥ እንዲህ ይለናል፡-
“ጌታችሁም፡- ብታመሰግኑ በእርግጥ እጨምርላችኋለሁ፣ ብትክዱም እቀጣችኋለሁ፤ ቅጣቴ በእርግጥ ብርቱ ነውና በማለት ባስታወቀ ጊዜ አስታውሱ።”
(ኢብራሒም፣ 7)
ምስኪኖችን፤ ቤተሰቦችንና ወዳጆችን መጠየቅ
ነብዩ በረመዳን ወር ቤተ - ዘመዶችን የመጠየቅ እና እንግዶችን ለፍጥሪያ የመጋበዝ ልምድ ነበራቸው፡፡ በተለይ ደግሞ ምንም የሌላቸውን ምስኪኖች በረመዳን ወር ያበሉ ነበር፡፡ አላህ በቁርአን ውስጥ እንዲህ ይላል፡-
“ሰይጣን እንዳትለግሱ ድህነትን ያስፈራራችኋል፤ በመጥፎም ያዛችኋል፤ አላህም ከእርሱ የሆነን ምህረትና ችሮታን ይቀጥራችኋል፤ አላህም ችሮታው ሰፊ፣ አዋቂ ነወ፡፡”
(አል - በቀራህ፣ 268)
ምህረት መሻት
አላህ የነብዩን ሐጢአት ሰርዞ ጀነትን ቃል ገብቶላቸዋል፡፡ ነገር ግን ነብዩ ሁልጊዜም ቢሆን የአላህን ይቅርታ ከመለመን ቦዝነው አያውቁም፡፡ በተለይ ደግሞ የበረከትና የምህረት በር ለሁሉም አማኞች በሚከፈትበት የረመዳን ወር ላይ፣ ከሌላው ጊዜ የበለጠ የአላህን ምህረት ይጠይቃሉ፡፡ አላህ በቁርአን ውስጥ እንዲህ ይላል፡-
“ከጌታችሁ ወደ ሆነችው ምህረት፤ መጠኗ እንደ ሰማይና ምድር ስፋት ወደሆነችው ገነት ተሽቀዳደሙ፤ ለነዚያ በአላህና በመልእክተኞቹ ላመኑት ተዘጋጅታለችና። ይህ የአላህ ችሮታ ነው፤ ለሚሻው ሰው ይሰጠዋል፤ አላህ የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነው፡፡”
(አል - ሐዲድ፣ 21)
ረመዳን ከሌላው ወር የተለየ የሚያደርገው የውስጥ ፍላጐታችን እንዲሟላ ለአላህ ፀሎትና ልመና የምናደርስበት ወር በመሆኑ ነው፡፡ ነብዩ ሙሐመድ በኢብን ማጃህ ሐዲስ ውስጥ እንዲህ ይሉናል፡-
“የእያንዳንዱ ፆመኛ ጸሎት በእያንዳንዱ ማፍጠሪያ ሰዓት ላይመለስ ያገኛል፡፡”
ባጠቃላይ በረመዳን ወር የነበረው የነብዩ ህይወት ይህን ይመስላል፡-
ቁርአንን መቅራት (ነብዩ ማንበብና መፃፍ ስለማይችሉ በአእምሯቸው ውስጥ ያለውን ነው የሚያነበንቡት)
ለሶላቶች ትኩረት መስጠት
ተጨማሪ የሱና ሶላቶችን መስገድ
የለሊት ሶላቶችን ማድረስ (ቂያሙል ለይል)
ምፅዋቶችን መስጠት
ከቤተሰብ ጋር ማሳለፍ
ምስኪኖችንና እንግዶችን ቤት መጋበዝ (ማስፈጠር)
ከአላህ ምህረት መሻት (መጠየቅ)
ዱአ (ፀሎት) ማድረግ
በመጨረሻ በነብዩ የአጐት ልጅ፣ አሊ ኢብን ጣሊብ ንግግር እንሰነባበት፡፡ አሊ በአል - ባይሐቂ ሐዲስ ውስጥ ነብዩን እንዲህ ጠየኳቸው ይለናል፡-
“የአላህ መልዕክተኛ ሆይ! በረመዳን ወር ምርጥ የተባለው ተግባር ምንድነው?” ነብዩ እንዲህ መለሱ፡- “አንተ አቡ ሐሰን ሆይ! በዚህ ወር ምርጥ የተባለው አላህ ከከለከለው ነገር መራቅ ነው፡፡”
በዚህ ቅዱስ ወር የአላህ ሰላም፣ በረከት እና ፍቅር በሐገራችን ላይ ይውረድ! አሚን፡፡

Published in ህብረተሰብ
  • ስንት ወላጅ፣ስንት ቤተሰብ፣ስንት ጓደኛ፣ስንቱ --- ተደሰተ!?
  •  በዚህ ሳምንት ብቻ 15 ወጣት ታሳሪዎች ከእስር ነጻ ወጥተዋል

    በዘንድሮ ምርጫ የሚዲያ ቅስቀሳ ላይ ኢዴፓ በEBC “ሳንሱር ተደርጐ” (በአዋጅ ከቀረ እኮ ዘመናት አልፈዋል!) ሳይተላለፍ ቀረብኝ ያለው አንድ የቅስቀሳ መልዕክት ባስታወስኩት ቁጥር ግርም ይለኛል። ለምን ይገርመኛል? ባለመተላለፉ! ብቻ ግን አይደለም፤ ምክንያቱ ባለመታወቁም ጭምር ነው። ይታያችሁ…ኢዴፓ መንግስት ሆኜ ከተመረጥኩ አለ በ if clause… “መንግሥት ሆኜ ከተመረጥኩ --- የፖለቲካ እስረኞችን በሙሉ እፈታለሁ”  ጉዳዩ የሚመለከታቸው የEBC ሃላፊዎች (ኢህአዴግም መንግስትም አያደርጉትም ባይ ነኝ!) ይሄ በሚዲያ መተላለፍ አይችልም ብለው ተፈጠሙ፡፡ (የደርግ “ሳንሱር” ያገረሸበት ኃላፊ እንደሚኖር ጠርጥሩ!) መፍትሔው ምን ቢሆን ጥሩ ነው? “ተስተካክሎ ይምጣ!” እግዜር ያሳያችሁ…ምኞት እንዴት ሆኖ ይስተካከላል! (የሆኖ ሆኖ የኢዴፓ ምኞት ሳንሱር ተደረገበት!)
እውነቱን ልንገራችሁ አይደል… መልዕክቱ ሊስተካከል የሚችለው እኮ፤ “ኢዴፓ መንግስት ሆኖ ከተመረጠ የፖለቲካ እስረኞችን በሙሉ ከእስር አይፈታም” በሚል ተቃራኒ ሃሳብ ብቻ ነው፡፡ (ሌላ መላ የለውማ!) እናላችሁ---ነገርዬው ግራ የሚያጋባ ነበር (እንኳን ለባለቤቱ ለ “ኢዴፓ” ለእኛም ጭምር!) ደግነቱ ግን የማያልፍ የለም---- ሁሉም አለፈ፡፡ (“እንዳያልፉት የለም ያ ሁሉ ታለፈ” አለ ብአዴን!) የምርጫ ቅስቀሳውም… የቦርዱ ማስፈራሪያም…የፓርቲዎች መዘላለፍም… የሰፊው ህዝብ  ፍርሃትም… የምርጫ ውጤቱም… ሁሉም ነገር ከሞላ ጐደል በሰላም ተጠናቋል - በምርጫ ቦርድ መግለጫ መሰረት፡፡
ወዳጆቼ፤ ይሄን ያለፈ የምርጫ ውዝግብ ያነሳሁት ጐዶሎአችንን ለማጉላትና ባለፈ ስህተት የEBCን ሃላፊዎች ለመውቀስ አስቤና አልሜ እንዳይመስላችሁ (ለነገሩማ ሥራዬ ተብሎ ሊወቀሱ ይገባቸው ነበር!) እኔ ጉዳዩን ለማንሳት ሰበብ የሆነኝ ግን ሰሞኑን የዞን 9 ሁለት ጦማሪያንና 3 ጋዜጠኞች (ከ1 ዓመት ከ 4 ወር እስር በኋላ መሆኑ ነው) ክሳቸው ተነስቶ ከእስር የመፈታታቸው ዜና ነው (ዜና ብቻ ያንስበታል ልበል!?) እስቲ አስቡት---በእኒህ ወጣቶች መፈታት ስንት ወላጆች ---- (በተለይ እናቶች!) በተስፋ ተሞልተው በደስታ እንደሚያነቡ? (እያነቡ እስክስታ አለ ቴዲ አፍሮ!!)
የሚገርመው ደግሞ ከወላጅም በላይ ብዙ ኢትዮጵያውያን በደስታ ጮቤ ረግጠዋል፡፡ (የልማታዊ መንግስታችን ግብም እኮ ለእኛ ሁለንተናዊ ደስታ ማጎናጸፍ ነው!) እናላችሁ --የመዲናዋ ድባብ ሁሉ ተቀይሮ ነው የሰነበተው፡፡ እኔ በበኩሌ---ከአንዳንድ ጭፍን የኢህአዴግ ካድሬዎች በቀር ለምን ተፈቱ በሚል ያጉረመረመ እንኳን አልገጠመኝም (ሰው ከእስር ሲፈታ ማጉረምረምማ ሰብዓዊነትም አይደለም!) እናላችሁ----መንግስት መፍታቱን እንዲለምድበት ጅምሩን እናድንቅለት፡፡ በነካ እጁ ታዲያ ቀሪዎቹንም ቢፈታቸው --- በቀጣዩ ምርጫ ድምጼን አሽረው ነበር፡፡ (ለነገሩ እኮ እንደ ኢህአዴግ ዕድሉን ላገኘ ያሰሩትን መፍታት ቢጠቅም እንጂ አይጎዳም!!)
በነገራችን ላይ በእነዚህ ወጣቶች መፈታት ያጉረመረሙ አንዳንድ “ፍሬሽ ካድሬዎች”ና ጭፍን ደጋፊዎችም ቀስ እያሉ መደሰታቸው አይቀርም። (እያፌዝኩ ከመሰላችሁ---በዚህ ፌዝ የለም!) ይሄውላችሁ----ልማታዊ መንግስታችን ልጆቹን በመፍታቱ አንድ ከባድ ዕዳ ከላዩ ላይ እንዳቃለለ ነው የምቆጥረው፡፡ (ማን ነበር “ሰነፍ መሪ ጭንቅላቱ ላይ ሸክም ያበዛል” ያለው?) እንዴት አትሉኝም? ከዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማትና ከጋዜጠኞች መብት ተከራካሪ ድርጅቶች የዘወትር ወቀሳ መጠነኛ እፎይታን ያገኛል፡፡ (ኢህአዴግ እፎይ ሲል ደግሞ አባላትና ደጋፊዎችም እፎይ ማለታቸው አይቀርም!)
እግረመንገዴን ግን ለኢህአዴግ በወዳጅነት የምለግሰው አንድ ምክር አለኝ፡፡ በፌስ ቡክ ላይ ፓርቲውን ደግፈው የሚጽፉ (የሚጽፉ የሚመስላቸው ቢባሉ ይሻላል!) “ፌስቡከሮች” ኢህአዴግ የመለመላቸው ከሆኑ ዳግም ምልመላውን መፈተሽ ሳይኖርበት አይቀርም፡፡ (ወይም መልማዮቹ መገምገም አለባቸው!) እንዴ----አብዛኞቹ እኮ እንኳንስ ሃሳብን በሃሳብ ሊመክቱ ቀርቶ ከማንበብና መፃፍ ደረጃ የዘለሉ አይመስሉም፡፡ ከምሬ እኮ ነው…የአስተሳሰብ ብስለትና ምጥቀት በሉት…የማሳመን ክህሎትና የአፃፃፍ ችሎታ--- ሲያልፍም አይነካቸው። ብቸኛ ሃብታቸው ጭፍን ድጋፍ ብቻ ነው፡፡ (ከ7 ሚሊዮን በላይ ደጋፊ አለኝ የሚል ፓርቲ እንዴት ጥሩ አውጠንጣኝ መመልመል ያቅተዋል!)
ወደ ዋና አጀንዳችን ስንመለስ…ፋና ሬዲዮ “ራሳቸውን ጦማሪያን የሚሉት…” በሚል የገለጻቸውን ወጣቶች መንግስት መፍታቱ (ማንም ምንም ይበለው!) እኔ ከልማታዊ መንግስት የሚጠበቅ ሰናይ ተግባር ነው ባይ ነኝ፡፡
አንዳንድ “ፍሬሽ ካድሬዎች”ም ነገርዬውን ከአገር ገጽ ግንባታ አንፃር ቢያዩት ነው የሚበጃቸው። (የአገር ገጽ በወሬ አይገነባም!) ዳያስፖራው የኦባማን የኢትዮጵያ ጉብኝት የሚቃወመው ለምንድነው? እነ ዋሺንግተን ፖስት ጉብኝቱን ያብጠለጠሉት በምን ሰበብ ነው? ፖለቲከኞች---ብሎገሮችና ጋዜጠኞች ያለአግባብ ታስረዋል----ገዢው ፓርቲ ምርጫውን በ100 ፐርሰንት ጠቅሎ ወሰደው--(ይሄ እንኳን ከአቅም በላይ ነው!) ወዘተ እያሉ አይደለም እንዴ? እናም መንግስት ልብ ገዝቶ የታሰሩትን ሲፈታ ማበረታታት እንጂ ማጉረምረም አይበጅም፡፡ ይልቅስ የቀሩትንም እንዲፈታ መገፋፋት ነው የሚገባው። (ለነገሩ ጥቅሙን እያየው ሲመጣ ማንም ሳይለው መፍታቱ አይቀርም!) ጥቅሙን ስላችሁ ደግሞ ሌላ ማለቴ እንዳይመስላችሁ፡፡ የህዝቡ መንፈስ ሲቀየር… የዓለምአቀፍ ሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ወቀሳና ጩኸት ሲቀንስ… በጋዜጠኞችና ፖለቲከኞች እስርና ወከባ ዙሪያ የሚሰነዘረው ክስና ስሞታ ሲበርድ እንዲሁም በምትኩ ምስጋናና ውዳሴ ሲዘንብለት… ኢህአዴግ ራሱ በዓመት ሁለት ሦስቴ እስረኞችን መፍታት እንደሚጀምር እገምታለሁ፡፡ (መገመት መብት ነው!)
በእርግጥ ኢዴፓ በምርጫ ቅስቀሳው ላይ እንዳለው፤ የፖለቲካ እስረኞችን በሙሉ በአንዴ አይፈታ ይሆናል (አገር መምራትና የምርጫ ቅስቀሳ ለየቅል ናቸው!) ግን አንዳንዶች እንደሚሉት…እኚህ ባራክ ኦባማ መለስ ቀለስ ካሉ፣ ቀስ እያለ መፍታቱ አይቀርም (ፈርቶ እኮ አይደለም!) ኦባማ የዲሞክራሲ እናት የምትባለው የአገረ አሜሪካ ፕሬዚዳንት በመሆናቸው ለክብራቸው ሲል ብቻ ያደርገዋል፡፡  በሌላ አነጋገር ለዲሞክራሲ ካለው ጥልቅ ክብር የተነሳ “የፖለቲካ እስረኞች”ን በሙሉ አንድ ቀን ፈትቶ፣ ወህኒ ቤቶቹን ኦና ባያደርገው ምን አለ በሉኝ፡፡ እንዴ…ኢህአዴግ ዕድሜ ዘመኑን የታገለው ሰዎች በፖለቲካ አመለካከታቸው የተነሳ እስር፣ ወከባ፣ ስደት፣ መገለል እንዳይደርስባቸውና በነፃነት ያሻቸውን የፖለቲካ ሃሳብ እንዲያንሸራሽሩ፣መብታቸውም ሙሉ በሙሉ እንዲከበርላቸው እኮ ነው፡፡ ግን ምን ያድርግ? ሥልጣን ላይ ሆኖ ሲያየው ጉዳዩ ሌላ ሆነበት፡፡ እንጂማ የኦባማ መምጣትም ባላስፈለገው ነበር፡፡ (የሆኖ ሆኖ ግን ኦባማ እግራቸው እርጥብ ነው!) አንዴ ሳይሆን ሺ ጊዜ ይምጡልን!!
እናላችሁ… አንዳንዶች መንግስት ብሎገሮቹንና ጋዜጠኞቹን የፈታው ኦባማ ስለሚመጡ ነው (“The Obama Effect?” የሚል ስያሜ ሁሉ አውጥተውለታል!) ብለው ሲመፃደቁ ሰምቼ ተገርሜአለሁ፡፡ (ኦባማ ባይሆኑ ኖሮ፣ ነጭ አምላኪዎች ልላቸው ከጅሎኝ ነበር!)
እኔ ግን ኦባማ ሰበብ ሆኑ እንጂ ዋናው የልማታዊ መንግስታችን ልበ -ቀናነት ነው ባይ ነኝ። የለም ኦባማ ናቸው ያስፈቱት ብሎ የሚፈጠም ካለ ግን ይሁንለት፤ደስ ይበለው! (መቻቻል እኮ ሌላ አይደለም!)
በነገራችን ላይ ከአገር ውስጥ ተቃዋሚዎች ያስደሰቱኝ----ኦባማ እንዲያነጋግረን እንፈልጋለን ብለው ለአሜሪካ ኤምባሲ በደብዳቤ የጠየቁት ናቸው (ፕራግማቲክ ይሏችኋል እንዲህ ነው!) እንዴ…! ምንስ ቢሆን እንደነ ዋሺንግተን ፖስት ኦባማን ወደ ጦቢያ ድርሽ እንዳይሉ ማብጠልጠል ከኢትዮጵያዊ ይጠበቃል እንዴ? ይልቁንስ በአካል መጥተው ልማቱንም --ባቡሩንም--ቤተመንግስቱንም---ወህኒቤቱንም-----ተቃዋሚውንም---የመንግስት ባለስልጣናቱንም--ሚዲያውንም---- ጐብኘት ጐብኘት አድርገው ቢመክሩን አይሻልም?  በነገራችን ላይ ኦባማ  በተቃውሞ ሰልፍና በጋዜጣ ነቀፋ የሚመሩ ቢሆን ኖሮ እግራቸውን ከዋይት ሃውስ አያነሱም ነበር፡፡ (ማን ነበር “ከኢያሪኮ ውጭ በጩኸት የፈረሰች ከተማ አናውቅም” ያለው?)

Saturday, 11 July 2015 11:56

የፀሐፍት ጥግ

የራሳችንን ጭብጦችና ታሪኮች ለመግለፅ
የምዕራባውያንን ዘይቤ ተጠቅመን ፅፈናል።
የሥነ ፅሁፍ ቅርሳችን ግን “አንድ ሺ አንድ
ሌሊቶች”ን እንደሚያካትት እንዳትዘነጉ፡፡
ናጂብ ማህፉዝ
· ጭብጦች በሥራዬ ላይ በተደጋጋሚ እያሰለሱ
ይመጣሉ፡፡
ኢቭ አርኖልድ
· ለእኔ ህይወት እና ሞት በጣም ወሳኝ ጭብጦች
ናቸው፡፡ ሞት በሌለበት ህይወት የለም፡፡ ለዚያ
ነው ለእኔ በጣም ወሳኝ የሆኑት፡፡
ቲቴ ኩቦ
· ለእኔ ጭብጥ፤ ፍቅርና የፍቅር እጦት ነው።
ሁላችንም ፍቅርን እንፈልገዋለን፡፡ ግን እንዴት
እንደሚገኝ አናውቅም፡፡ እያንዳንዱ ድርጊታችን
እሱን ለመጨበጥ የሚደረግ ሙከራ ነው፡፡
ርያን ጐስሊንግ
· እውነት አንድ ብቻ ብትሆን ኖሮ፣ በተመሳሳይ
ጭብጥ መቶ ሸራዎች ላይ አትስልም ነበር፡፡
ፓብሎ ፒካሶ
· የእንግሊዝ ገጠራማ ክፍል እድገትና ውድመት
እውነተኛና አሳዛኝ ጭብጥ ነው፡፡
ኢ.ኤም.ፎርስተር
· አገራት ገንዘብ በመፈለጋቸው የተነሳ ባህላቸውን
አጥተዋል፡፡ በየአገሩ ገንዘብ የወቅቱ ጭብጥ
የሆነበት ጊዜ ነበር፡፡ በዚህም ሳቢያ ባህል
መስዋዕት ተደረገ፡፡
ዩኮ ኦኖ
· አንድ ጭብጥ ውሰድና አድምተህ ስራው …
ጉዳዩ ታዲያ አንድም ከልብህ የምትወደው
አሊያም ከልብህ የምትጠላው መሆን አለበት፡፡
ዶሮቲያ ላንጅ
· ፍቅር፤ በሥራዬ ላይ እየተመላለሰ የሚመጣ
ጭብጥ ነው፡፡
ትሬሲ ቻፕማን
· ቁጭ ብዬ በሴራ እና ጭብጥ መካከል ያለውን
ልዩነት አስቤ አላውቅም፡፡ ለእኔ ያ ጨርሶ
አስፈላጊ ሆኖ አያውቅም፡፡
ሌን ዌይን
· ፀሐፊያን ቁጭ ብለው ስለ አንድ ዓላማ ወይም
ጭብጥ አሊያም ስለሆነ ነገር ለመፃፍ ማሰብ
ያለባቸው አይመስለኝም፡፡ ስለራሳቸው
የህይወት ተሞክሮ ከፃፉ፣ አንድ የሆነ እውነት
ብቅ ይላል፡፡
ዶሪስ ሌሲንግ
· ያለጥርጥር የምማረክበት ጭብጥ ሞት ነው።
አላን ቦል
· ጭብጥህ ውሎ አድሮ ያገኝሃል፡፡ አንተ እሱን
ፍለጋ መውጣት አይኖርብህም፡፡
ሪቻርድ ሩሶ
· ፊልም ሰ ሪዎች፤ “ ስለዚህ ጉ ዳይ ወ ይም በ ዚህ
ጭብጥ ላይ ፊልም መስራት እፈልጋለሁ” ይላሉ፡
፡ እኔ ግን ፈፅሞ እንደዚያ ብዬ አልጀምርም፡፡
አንድሪያ አርኖልድ


Published in ጥበብ

‹‹ማንም ሰው ሊገምት እንደሚችለው፤ ንጉሡ ለሉዓላዊ የንጉስነት መብታቸው ፍፁም ቀናተኛ ናቸው፡፡
ይህን ሉዓላዊ ሥልጣናቸውን በሆነ መንገድ የሚነካ በመሰላቸው ጉዳይ ላይ መለሳለስ አያውቁም--”

የመጨረሻው ክፍል
አውሮፓውያን ለጥቁር ህዝብ ያላቸው ንቀት የበዛ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ፤ ቀና አመለካከት እና ከቴዎድሮስ ጋር ጥብቅ ወዳጅነት ያለው ፕላውዴን ወደ ለንደን ይልከው የነበረው መልዕክት እንኳን፤ ይኸው መጥፎ ንቀት የሚታይበት ነበር፡፡ የአክብሮት ሐሳቦችን በያዙት በእኒያ የፕላውዴን ደብዳቤዎች ውስጥ የአውሮፓ በሽታ የሆነውን የንቀት ስሜት በግልፅ ማየት ይቻላል፡፡
‹‹ማንም ሰው ሊገምት እንደሚችለው፤ ንጉሡ ለሉዓላዊ የንጉስነት መብታቸው ፍፁም ቀናተኛ ናቸው። ይህን ሉዓላዊ ሥልጣናቸውን በሆነ መንገድ የሚነካ በመሰላቸው ጉዳይ ላይ መለሳለስ አያውቁም፡፡ ሆኖም፤ በእኩያነት አቋም ከምዕራብ ኃያላን መንግስታት ጋር ግንኙነት የመመስረት ከፍተኛ ፍላጎት ያላቸው ሲሆን፤ በቅርቡ አምባሳደሮቻቸውን ወደ እነዚህ ሀገራት የመላክ ሐሳብ አላቸው›› ሲል ለሐገሩ መንግስት ደብዳቤ የላከው ፕላውዴን፤ አክሎ፤ ‹‹አስቸጋሪ የሆነው ዓመላቸው የሚመነጨው ከዚሁ ቀናተኛነታቸው ነው፡፡ አለማወቅን እየተመገበ የሚፋፋው ኩራታቸው፤ በዓለም ላይ እንደሳቸው ያለ ታላቅ ንጉሥ መኖሩን ለመቀበል የሚቸገሩ ሰው አድርጓቸዋል›› በማለት ፅፏል፡፡
እርግጥ፤ አፄ ቴዎድሮስን፤ የለውጥ አራማጅ እና ባለራዕይ መሪ አድርገው የሚመለከቱ ፀሐፊዎች የመኖራቸውን ያህል፤ ይህን የማይቀበሉና አፄ ቴዎድሮስ የዘመነ መሳፍንት የመጨረሻው መሪ እንጂ የአዲስ ዘመን አዋጅ ነጋሪ መሪ አይደሉም በሚል የሚከራከሩ መኖራቸው የሚካድ አይደለም፡፡ እንደ ሪቻርድ ፓንክረስት እና ዶናልድ ክረሚ ያሉ የታሪክ ፀሐፊዎች ግን፤ ‹‹አፄ ቴዎድሮስ፤ የዘመናዊ ኢትዮጵያ የታሪክ የመጀመሪያው ምዕራፍ ገላጭ መሪ እና የዘመናዊት ኢትዮጵያ አባት ናቸው›› ይላሉ፡፡
የአፄ ቴዎድሮስን ታላቅ የጦር ሰውነት፣ በቅፅበት የመወሰን ችሎታ እና አስተዋይነት ብቻ ሣይሆን፤ ታላቅ ህልም የነበራቸው መሪ መሆናቸውን በርካታ ፀሐፊዎች ይመሰክራሉ፡፡ ሆኖም፤ በተከታታይ በተቀዳጁት ወታደራዊ ድል በተወሰነ ደረጃ የሐገሪቱን አንድነት ማረጋገጥ ቢችሉም፤ በተከታታይ ያገኙትን ወታደራዊ ድል ለማደላደል እና የኢትዮጵያን ዕድገት የሚያግዝ ሁኔታ ለመፍጠር የሚያስችል ዕውቀት እና ችሎታ እንዳልነበራቸው ይገልፃሉ፡፡ በእንግሊዛዊያን የታሪክ ፀሐፊዎች እና ጋዜጠኞች አስተያየት፤ ለንጉሡ ጥሩ መካሪ እና ዘካሪ ነበሩ የሚባሉት ባለቤታቸው የወ/ሮ ተዋበች እና እንግሊዛዊው ወዳጃቸው ጆን ቤል እና ፕላውደን በሞት መለየታቸው ብዙ ጎድቷቸዋል፡፡ ከዚያ በኋላ መካሪ አጥተው፣ ሁሉን ጠርጣሪ ሆነው፣ በቅፅበታዊ ስሜት የሚገፉ እና ያለ ምክር የሚወስኑ እየሆኑ በመሄዳቸው ብዙ ነገር እንደተበላሸም ያመለክታሉ፡፡
ፕላውዴን፤ ገና አፄ ቴዎድሮስ ስልጣን ከመያዛቸው በፊት፤ በራስ ዓሊ ዘመን በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ቆንስላ ሆኖ ቆይቶ፤ ‹‹እንግሊዝ ከኢትዮጵያ ጋር የንግድ ግንኙነት ብትመሰርት ተጠቃሚ ትሆናለች›› የሚል ሐሳብ ለእንግሊዝ መንግስት አቅርቦ ጉዳዩ ስለታመነበት የንግድ ስምምነት እንዲፈራረም ወደ ኢትዮጵያ ተልኮ ነበር። ከቴዎድሮስ በፊት ከራስ ዓሊ ጋር የንግድ ስምምነት ለመፈራረም ጥረት ሲያደርግ፤ ራስ ዓሊ ‹‹አሁን ይኸ ምን ይረባል ብለህ ነው›› እያሉ ፍፁም ደስ ሳይላቸው ከፕላውዲን ጋር የንግድ ስምምነት ቢፈራረሙም፤ ብዙ ሳይቆዩ በአፄ ቴዎድሮስ ስልጣናቸው ተነጠቀ፡፡
ፕላውዲን ከአፄ ቴዎድሮስ ጋር ተመሣሣይ የንግድ ስምምነት ለማድረግ ብዙ ቢደክምም፤ አፄ ቴዎድሮስ እምቢ አሉት፡፡ አፄ ቴዎድሮስ ከፕላውዴን ጋር የጠበቀ ወዳጅነት ቢኖራቸውም ከእንግሊዝ ጋር የንግድ ስምምነት ለመፈራረም ፈቃደኛ አልነበሩም፡፡ የኢትዮጵያ ነገስታት አውሮፓውያንን በጥርጣሬ ይመለከቱ ስለነበር፤ በዚህ የተነሳ፤ ራስ ዓሊም ሆኑ አጼ ቴዎድሮስ የአውሮፓ ቆንስሎች በኢትዮጵያ ምድር እንዲቀመጡ ፈቃደኞች አልነበሩም፡፡ ስለዚህ፤ የአምባሳደር ተልዕኮ የነበራቸው አውሮፓውያን መቀመጫ የቱርክ ግዛት የነበረችው ምፅዋ ነበረች፡፡
በስምምነቱ አለመፈረም የተበሳጨው የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት፤ ‹‹በአስቸኳይ ወደ ምፅዋ እንድትወርድ ይሁን›› የሚል ትዕዛዝ በመላኩ፤ ፕላውዴን በወቅቱ በቱርክ እጅ ወደ ነበረው ምፅዋ ሲወርድ በመንገድ ያደፈጡ ሽፍቶች ተኩሰው አቆሰሉት፡፡ በዚሁ ጥቃት ክፉኛ የቆሰለው ፕላውዴን በ1860 ዓ.ም (እኤአ) ለሞት በቃ፡፡
ከዚያ በኋላ፤ ንጉሡ በማንንም ላይ እምነት ማሳደር የማይችሉ ሰው በመሆናቸው፤ እርሳቸው እንደተመኙት፤ የኢትዮጵያ መድኅን በመሆን ፋንታ አጥፊ የሆኑበት ሁኔታ እንደ ተፈጠረ እና ሠራዊታቸውም በህዝቡ ዘንድ መርገምት እና ስጋት ሆኖ መታየት መጀመሩንም የታሪክ ፀሀፊዎች ያወሳሉ፡፡ የአፄ ቴዎድሮስ ሠራዊት ለዘመቻ ወጥቶ ሲመለስ፤ በየጊዜው ቁጥሩ እየጨመረ ስለሚሄድ፤ በመንግስት ግምጃ ቤት በነበረው ሐብት ለመተዳደር የማይችል እየሆነ በመምጣቱ፤ የሠራዊቱን ቀለብ ለመሸፈን ሲባል በቤተክህነት እጅ ይገኝ የነበረን ጦም የሚያድር መሬት መውሰድ ጀመሩ፡፡ እንዲሁም ከህዝቡ መሬት እየነጠቁ፤ የቤት የለሽ እና የስርዓተ - አልበኛውን ሰው ቁጥር ከፍ አደረጉት ይላሉ፡፡                
በአፄ ቴዎድሮስ ዘመን፤ ለስብከት የመጡ አውሮፓዊ የኢየሱሳውያን፣ የፕሮቴስታንት እና የካቶሊክ ቄሶች  በኢትዮጵያ ይኖሩ ነበር፡፡ ሆኖም፤ አፄ ቴዎድሮስ ከአውሮፓ ይፈልጉ የነበረው ሰባኪዎችን ሳይሆን ሙያተኞችን ነበር፡፡ አፄ ቴዎድሮስ እንዲያ የሚጠሏቸውን ሚሲዮናውያንን በሐገራቸው እንዲኖሩ የፈቀዱት ጥበብን ፍለጋ ነበር፡፡ የሐይማኖት ሰዎቹን የሚጠሏቸው በሁለት ምክንያቶች ነው፡፡ አንድም፤ አፄ ቴዎድሮስ ለኢትዮጵያውያን ከኦርቶዶክስ ሌላ ተመራጭ ሐይማኖት የለም ብለው ያስቡ ስለ ነበር ነው፡፡ አንድም፤ የተለያዩ ሐይማኖቶች መኖር የሐገሪቱን ህዝብ ለክፍፍል እና ለግጭት የሚዳርግ ችግር ይፈጠራል የሚል እምነት ስለነበራቸው ነው፡፡
በተለያዩ የክርስትና ሐይማኖት ተከታዮች መካከል ፉክክርና ፍትጊያ ተፈጥሮ ብዙ ችግር መፈጠሩን የሚያወሱ አውሮፓውያን ፀሐፊዎች፤ የእነዚህ ተፎካካሪ ሐይማኖቶች አድራጎት በኢትዮጵያ ላይ ዘመን የተሻገረ ተፅዕኖ አስፍሯል ይላሉ፡፡ በአጠቃላይ ለውጭ ሰዎች (ክርስትያን ቢሆንም ባይሆንም) ጥላቻና ጥርጣሬ እንዲያድርባቸው አድርጓል ሲሉም ፅፈዋል፡፡ ‹‹አበሾች መሠሪ፣ ተጠራጣሪ እና ቀናተኞች ናቸው›› የሚሉት እነኚሁ ፀሐፊዎች፤ ‹‹ጃዝዊቶች፤ በርካታ ምዕተ ዓመታት ማለፍ እንዲዘነጋ ያላደረገውን ትምህርት አስተምረዋቸዋል ሄደዋል›› በማለት አስተያየታቸውን አስፍረዋል፡፡  
አፄ ቴዎድሮስ፤ አውሮፓውያኑ ሰባኪዎች፤ ፈላሾችን (ቤተ-እስራኤላውያን) እና የክርስትና ሐይማኖት ተከታይ ያልሆኑ ኢትዮጵያውያንን እንዲሰብኩ የፈቀዱ ቢሆንም፤ ወደ ክርስትና የሚገቡትን ሰዎችን የሚያጠምቁት ግን የኦርቶዶክስ ካህናት ብቻ እንዲሆኑ አድርገዋል። ፕሮቴስታንት እና ካቶሊኮቹ ቄሶች እንዲሰብኩ እንጂ እንዲያጠምቁ አልፈቀዱላቸውም፡፡ በአንፃሩ፤ ሚሲዮናውያኑ ጋፋት ላይ የማይፈልጉትን ምድራዊ ተግባር በማከናወን የተጠመዱት፤ ‹‹ውሎ - አድሮ፤ አጼ ቴዎድሮስ እንደ ልብ እንድንሰብክ ይፈቅዱልን ይሆናል›› በሚል ተስፋ ነበር፡፡
ሆኖም፤ የአጼ ቴዎድሮስ ዋና ፍላጎት ሙያተኛ ከሆኑት አውሮፓውያን ዕውቀቱን በመቅሰም፤ የሐገሪቱን የቴክኖሎጂ አቅም በመገንባት፤ ኢትዮጵያን ከውጭ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ጥገኝነት ነፃ ማውጣት እንደ ነበር ምሁራን ይጠቅሳሉ፡፡ ‹‹ቴዎድሮስ ከውጭ የሚመጣባቸውን ጫና ለመቋቋም፤ በቅድሚያ ህዝባቸውን መለወጥ እና ማሻሻል በጣም አስፈላጊ መሆኑን የተረዱ የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ንጉስ ናቸው›› የሚሉት ዶናልድ ክረሚ፤ የአፄ ቴዎድሮስ ሐገርን የማዘመን ጥረት ትኩረት ያደረገው፤ ነባሩን የሐገሪቱን ህግ መሠረት አድርገው በመንግስት እና በቤተክህነት መካከል አንድነት በመፍጠር፣ ለረጅም ጊዜ በዘለቀ ጦርነት ፈራርሰው የጠፉትን ነባር መንግስታዊ ተቋማት እንደገና በማቆም፣ የህዝቡን ሞራላዊ አቋም በማሻሻል እና ሠራዊቱን በተሻለ መሠረት መልሶ በመገንባት፤ እንዲሁም ከአውሮፓ ሐገራት ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በመመስረት ላይ እንደነበርም ያመለክታሉ፡፡
‹‹የአፄ ቴዎድሮስ ውድቀት እና ምናልባትም ኃይለኝነት ለሚንፀባረቅበት ባህርያቸው መነሻ ምክንያት የሆነው፤ በህግ የበላይነት ላይ በተመሠረተ አሰራር ሥልጣንን ለሌሎች ማከፋፈል አለመቻላቸው ነው›› የሚሉት ዶናልድ ክረሚ፤ ‹‹በዚህ የተነሳ አፄ ቴዎድሮስ፤ ሐገር ከመምራት እና ህዝብን ከማስተዳደር ይልቅ፤ የአመጽ እሳትን በማጥፋት ጊዜያቸውን ጨርሰዋል›› ሲሉ ፅፈዋል።
እንደ ዶናልድ ክረሚ ያሉ አንዳንድ የታሪክ ፀሐፊዎች፤አፄ ቴዎድሮስ አውሮፓውያኑ የሚያሳይዋቸው ዝቅተኛ ግምት፤ በእነሱ መካከል ይታይ የነበረው የውስጥ ሽኩቻ እና ትንቅንቅ፤ እንዲሁም ፖለቲካዊ ሴራቸው በተለያየ መልክ እየተገለጠ፤ ግራ እንዲጋቡና ትኩረታቸውን እንዲረበሽ አድርጎታል ይላሉ፡፡
የአውሮፓውያን የፖለቲካ አጋርነት በምን ላይ እንደሚመሰረት ያልተረዱት እና በ‹‹ክሪሚያው›› ጦርነት (Crimean war) ‹‹ክርስቲያናዊ ሐገራት›› ብለው የሚያስቧቸው ፈረንሳይ እና እንግሊዝ፤ ኢስላማዊ አድርገው ከሚመለከቷት ቱርክ ጋር አብረው፤ ሌላዋን ክርስቲያናዊ ሐገር ሩሲያን ለማጥቃት መሰለፋቸው፤ ለአፄ ቴዎድሮስ በጣም ግራ አጋቢ ጉዳይ ነበር፡፡ የፖለቲካ አጋርነት በሐይማኖት ላይ ብቻ እንደማይመሠረት ያልተረዱት አፄ ቴዎድሮስ፤ ይህን የአውሮፓውያን ድርጊት ለመረዳት ወይም ለመቀበል ተቸግረዋል፡፡
አፄ ቴዎድሮስ በምዕራባውያኑ ነገር ግራ የሚጋቡትን ያህል፤ በአካል የሚያውቋቸው ምዕራባውያንም በአፄ ቴዎድሮስ ዓመል በእኩል ደረጃ ግራ ይጋቡ ነበር፡፡ ፍፁም ደግ እና ርኅሩህ ሰው ናቸው ለማለት የጀመሩትን ዓረፍተ ነገር ሳይጨርሱ፤ ፍፁም ጨካኝ እና አረመኔ ሊሏቸው ይገደዳሉ፡፡ አንድም ቀን እንደ ንጉስ ክብር እና ማዕረግ ያለው ኑሮ ሳይመኙ የህዝባቸውን ህይወት ለመለወጥ ከተራ ሰው የማይሻል ኑሮ እየኖሩ ዘመናቸውን የገፉ፤ አጥፍቻለሁ ማለት የማይከብዳቸው፣ በኃይማኖተኛ ሰው ዘንድ ሊታይ የሚችል ትህትና ያላቸው ሰው ብለው ከጀመሩ በኋላ፤ መልሰው ‹‹ከእኔ በላይ ታላቅ ንጉሥ የለም ባይ ናቸው›› በማለት ለመደምደም የሚሞክሩ ናቸው፡፡ አሁን፤ ‹‹እንደ ባህር የሰፋ ትዕግስት ያላቸው መሪ ናቸው›› ብለው፤ መልሰው፤ ‹‹ድንገት በቁጣ ቱግ የሚሉ እና መረን የለቀቀ ስሜታዊነት የተጠናወታቸው መሪ ናቸው›› የሚል ቃል ለመናገር የሚያስገድዱ ሆነውባቸው ተቸግረው ነበር፡፡  
የጨርቅ ነጋዴ ልጅ ለሆነው እና በአፍሪካ የተመቸ መኖሪያ ለማግኘት ሲንከራተት ገንዘቡን የጨረሰው ሄንሪ ዱፍተን፤ ሊጅን (LeJean) የተባለ የሐገሩ ሰው፤ በኢትዮጵያ የፈረንሳይ ቆንሲል ሆኖ ተልኮ ወደ ኢትዮጵያ ሲጓዝ አግኝቶት፤ እሱን ተከትሎ ኢትዮጵያ መግባቱን የሚገልፁት የታሪክ ፀሐፊዎች፤ ‹‹አጼ ቴዎድሮስ፤ ዱፍተን ገንዘብ አጥቶ መቸገሩን ሲሰሙ በታላቅ ቸርነት እና ደግነት ተቀብለውት አስተናገዱት›› በማለት የአፄ ቴዎድሮስን ደግነት እና ርህራኄ ያትታሉ፡፡
አፄ ቴዎድሮስ ለፈረንሳይ መንግስት ለላኩት ደብዳቤ ገና መልሱ ሳይመጣ፤ ‹‹የኢትዮጵያ ኑሮ የሰለቸው ሊጅን ‹ወደ ሐገሬ መሄዴ ነው› ብሎ ቢነሳ፤ አፄ ቴዎድሮስ አሰሩት፡፡ ለአንድ ቀን ካሰሩት በኋላ፤ በማግስቱ ከእስር ቢለቁትም፤ ወደ ፈረንሳይ ለላኩት ደብዳቤ ምላሽ እስኪያገኙ ድረስ ከሐገር እንዳይወጣ ከለከሉት፡፡ በመጨረሻም፤ ብራድል የተባለ ሰው ደብዳቤ ይዞ መጣ፡፡ ፈረንሳይ ብራድልን ምላሽ አስይዛ ብትልከው፤ የፈረንሳይ መልዕክተኛ ሆኖ እንዲሰራ ግን ፈቃደኛ አልነበረችም። በዚያን ጊዜ ንጉሱ፤ ሊጅንን ሰድበው፤ በኦክቶበር 2፣ 1863 ዓ.ም (እኤአ) ከሀገር እንዲወጣ አዘዙት›› በማለት ቁጡና ስሜታዊ አድርገው ይገልጧቸዋል፡፡
ዱፍተንም፤ ቻርልስ ዲከን ካሜሩን የተባለው የእንግሊዝ ቆንስላ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ አራት ወራት ካሳለፈ በኋላ ኢትዮጵያን ለቅቆ ሄደ የሚሉት የታሪክ ፀሐፊዎች፤ አዲስ የእንግሊዝ መንግስት አምባሳደር ሆኖ የመጣው ካሜሩን ወታደር እና ከፍተኛ ልምድ የነበረው ዲፕሎማት መሆኑን ያወሳሉ፡፡
አፄ ቴዎድሮስ፤ እንግሊዝ የምትፈልገውን የንግድ ስምምነት ለመፈራረም ከፕላውዴን የተሻለ ጥረት ሊያደርግ ይችላል የሚል እምነት በሀገሩ መንግስት የተጣለበትን ካሜሮንን አልወደዱትም፡፡ በውስጡ ያለውን ንቀት ላለማሳየት የማይጠነቀቀው ካሜሩን ከተቀመጠበት ሳይነሳ ደብዳቤ ሲሰጣቸው፤ ፂሙን በእጁ እየሞዠቀ ሲያናግራቸው በጣም ይበሳጩ ነበር፡፡ የእንግሊዙ መልዕከተኛ ካሜሮን፤ ከተቀመጠበት ሳይነሳ ለንጉሱ ደብዳቤ መስጠቱን፤ ከእንግሊዝ መንግስት እንዲያደርስ የተሰጠውን ደብዳቤ በሰው ልኮ ምፅዋ እና ከሰላ ሲንገላወድ ከርሞ የመምጣቱን ጉዳይ ምዕራባውያን የታሪክ ፀሐፊዎች፤ ከተለያየ የጤና ችግር ጋር ሊያይዙት ቢሞክሩም፤ የካሜሮን ዋናው ችግር አውሮፓዊ የንቀት በሽታ ነበር፡፡   
አፄ ቴዎድሮስ፤ በዘመነ መሳፍንት የተከፋፈለችውን ኢትዮጵያ አንድ ለማድረግ ቻሉ፡፡ ግን ከጦርነት ጨርሶ መውጣት ወይም አመጽ ከማዳፈን ሥራ በመገላገል የመሪነት ሚናቸውን ለመጫወት የሚያስችል ዕድል ሳያገኙ እንዲሁ እንደባከኑ ዘመናቸውን አሳለፉ፡፡ በወቅቱ፤ አረቦች እና ቱርኮች ከተለያዩ አቅጣጫዎች የሀገራቸውን ድንበር በመግፋት ላይ ነበሩ፡፡ ስለዚህ፤ በሩቅ ያለችውን ኢየሩሳሌምን ከያዙት እና ድንበራቸውን እየገፉ ከሚያስቸግሯቸው ቱርኮች እና አረቦች ስጋት የሚገላግል እና ሐገራቸውን ለመከላከል የሚያግዝ ወታደራዊ እርዳታ ሊሰጣቸው የሚችል ክርስቲያናዊ መንግስት አጥብቀው ይሹ ነበር፡፡
ይህን ዓላማቸውን ለማሳካት፤ አምባሳደሮቻቸውን ወደ እንግሊዝ የመላክ ሐሳብ እንዳላቸው በመግለፅ ለንግስት ቪክቶሪያ ደብዳቤ ፃፉ፡፡ ሆኖም ለደብዳቤያቸው ምላሽ አላገኙም፡፡ የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ደብዳቤውን ገፋ አድርጎ ረሳው፡፡ ከኢምፓየሩ አጠቃላይ ፖሊሲዎች እና አጣዳፊ ጥቅሞች ጋር አገናዝቦ፤ ለአፄ ቴዎድሮስ ደብዳቤ ምላሽ የመስጠቱን ጉዳይ ያን ያህል አስፈላጊ ሆኖ አላገኘውም፡፡ ስለዚህ፤ ሣጥን ውስጥ ወርውሮ ረሳው፡፡
አፄ ቴዎድሮስ ቅር አላቸው፡፡ ክብራቸውን የሚነካ አድራጎት ሆኖ ታያቸው፡፡ ስለዚህ ለእንግሊዞች ንቀት አፀፋ ለመስጠት እና የእንግሊዝ መንግስት ምላሽ እንዲሰጥ ለማስገደድ ሲሉ የእንግሊዝን ቆንስላ ካሜሩንን ጨምሮ ወደ 70 የሚደርሱ አውሮፓውያንን ሰብስበው ወህኒ አወረዷቸው፡፡ ከዚያ የእንግሊዝ ልዑክ መሪ ሆኖ ሆርሙደዝ ራሳም መጣ፡፡ እሱንም አሰሩት፡፡ የመቅደላ ዘመቻ ተፀነሰ፡፡
የማያልቅ ወሬ ጀምሬ ተቸገርኩ፡፡
ስለዚህ፤ ከዚህ በላይ ጊዜአችሁን እና የጋዜጣውን ገፅ መውሰድ አልሻም፡፡ ይሁንና አንድ ነገር ሳልናገር መደምደም አልፈልግም፡፡ እርሱም፤ የጀነራል ናፒር የመቅደላ ዘመቻ ከብዙ ምጥ እና ልዩ ዝግጅት በኋላ የተደረገ መሆኑ ነው፡፡ እንግሊዝ እንደ መቅደላው ዘመቻ ብዙ ያሰበችበት እና የተጨነቀችበት ጦርነት አለመሆኑንም የታሪክ ፀሐፊዎች ይጠቅሳሉ፡፡ በእስረኞቹ ቤተሰቦች እየተላኩ፤ በወቅቱ በነበሩት የእንግሊዝ ጋዜጦች ይታተሙ የነበሩትና አንዳንዴም የፈጠራ ሊሆኑ የሚችሉት የኢትዮጵያ እስረኞች ታሪክ፤ የእንግሊዝ መንግስት እና ህዝብ ለእስረኞቹ (በኋላም ለጦርነቱ) የተለየ ትኩረት እንዲሰጡ አድርጓቸዋል፡፡ ህዝቡ ጉዳዩን ልዩ ትኩረት ሰጥቶ መከታተል በመጀመሩም የጋዜጦች ተነባቢነት እንዲጨምር አደረገው፡፡ አልፎ ተርፎ፤ የእንግሊዝ መንግስት ባይወደውም ለዘመቻ እንዲዘጋጅ ከፍተኛ ጫና አሳደረበት፡፡ የኢትዮጵያ እስረኞች ጉዳይ፤ የእንግሊዝ እና የሌሎች ሐገራት የህዝቦችን ቀልብ እንደሳበ የተመለከቱት ጋዜጦችም፤ ከጀነራል ናፒር ወደ መቅደላ በመሄድ ዘገባዎችን የሚልኩ ጋዜጠኞችን ለመላክ እንዲወስኑ አደረጋቸው፡፡ የጦርነት ዘገባም እንዲህ ተጀመረ፡፡


Published in ህብረተሰብ

በጋዜጣችሁ የሰኔ 13 ቀን 2007 ዓ.ም ዕትም ላይ አልፋ የትምህርትና ስልጠና አ.ማህበርን በተመለከተ ባቀረባችሁት ዜና፤ “ቅሬታው” በአንድ ግለሰብ የቀረበ መሆኑ እየታወቀ “የአልፋ ባለ አክስዮኖችና አመራሮች እየተወዛገቡ ነው” የሚል ርዕስ መስጠታችሁ አሳሳች፣ ለጋዜጣው አንባቢያን ስለ አክስዮን ማህበሩ የተዛባ መግለጫ የሚሰጥና የአክስዮን ማህበሩን መልካም ስምና ዝና የሚያጐድፍ አቀራረብ በመሆኑ በብዙኃን ባለአክስዮኖች ዘንድ ጥያቄ አስነስቷል፡፡
በተጨማሪም በዘገባችሁ፣ በማንኛውም የበጀት ዓመት በአክስዮን ማህበሩ ተገኝቶ የማያውቀውን ብር 30.000.000 (ሰላሳ ሚሊዮን ብር) የተጣራ ትርፍ ማስረጃ ባላገናዘበ ሁኔታ ተገኝቶ ነበር ብላችሁ መግለፃችሁ እንዲሁም በ2006 በጀት ዓመት የተገኘው የተጣራ ትርፍ ብር 4.5 ሚሊዮን እንደሆነ ተገልፆ እያለ፣ በመጨረሻው በጀት ዓመት ብር 1.5 ሚሊዮን ብቻ እንደተገኘ አድርጋችሁ ማቅረባችሁና ቅሬታ አቅራቢው የገለፀውን አመራሩ ከሰጠው መልስ ጋር በማነፃፀር አለመዘገባችሁ ቅሬታ እንደፈጠረብን ልንገልፅ እንወዳለን፡፡
(ቢኒያም ሀይሉ የዳይሬክተሮች ቦርድ ፀሐፊ)

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 11 July 2015 11:52

“ወይ ጊዜ፣ ወይ ጊዜ…”

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
እናት ልጇ እስር ቤት ነው፡፡ እናም አንዳንድ የቤት ሥራ የሚያግዛት ሰው አጥታ ተቸግራለች፡፡ ታዲያላችሁ…ለልጇ ደብዳቤ ትጽፋለች፡፡
“የተወደድከው ልጄ፣ አንተ ከታሠርክ በኋላ ኑሮ በጣም ከብዶኛል፡፡ የጓሮ አትክልት ስፍራውን የሚቆፍርልኝ ሰው አላገኘሁም፡፡ ድንችና ቲማቲሙን መትከል አልቻልኩም…” ብላ ትጽፍለታለች፡፡ ልጁም…
“እማዬ፣ እባክሽ እሱን የአትክልት ስፍራ አትነካኪው። ከቆፈርሽው ፖሊሶች ይመጡና አንቺንም ያስሩሻል፣ የእኔም የእስር ዘመን ይራዘማል…” ሲል ይጽፋል፡፡ ከጥቂት ቀናት በኋላ እናት መልሳ ትጽፍለታለች፡፡
“አንተ ከጻፍክልኝ ደብዳቤ ጋር ፖሊሶቹም አብረው መጡ፡፡ የጓሮ አትክልት ስፍራውን ከዳር ዳር ቆፈሩት፡፡ ግን ምንም ነገር አላገኙም፡፡ ተበሳጭተው ነው የሄዱት፡፡” ልጁ ምን ብሎ ቢጽፍ ጥሩ ነው…
“እማዬ፣ ያው የተቻለኝን አድርጌያለሁ፤ አሁን ድንችና ተማቲምሽን መትከይ ትችያለሽ፡፡” አሪፍ አይደል! እሱም የእስር ዘመኑ አይራዘምበትም፡፡
ስሙኝማ…የጊዜ መራዘም ነገር ከተነሳ አይቀር…‘ጊዜ’ እኛን ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት ላቅርብ ቢል የክስ ሰነዱ በስንትና ስንት ስካኒያ ተጭኖ እንደሚሄድ አንድዬ ይወቀው፡፡ እናማ…‘ጊዜ’ እና አንድ የአገር ልጅ ቢነጋገሩ እንደሚከተለው የሚባባሉ ይመስለኛል፡፡
አያ ጊዜ፣ እንደምነህ?
እንደምን እንድሆን ትፈልጋለህ? እኔ’ኮ የሚገርመኝ ከጠባያችሁ የድፍረታችሁ!
ምን አጠፋሁ?
አየህ፣ ይሄን ነው የምልህ፣ ምን አጠፋሁ ትለኛለህ?
አያ ጊዜ፣ አልገባኝም…
ሁለት ሰዓት ቀጥረኸኝ ሦስት ሰዓት ትመጣለህ!
ውይ… ለእሱ ነው እንዴ እንዲህ የተበሳጨኸው! የሀበሻ ቀጠሮ ነዋ! ሀበሻ መሆኔን ረሳኸው እንዴ፣ ደግሞ አንድ ሰዓት ብቻ ነው የዘገየሁት፡፡ ምን አላት! እኔ እንደውም ቀጠሮ ላይ ቶሎ በመምጣት ነው የምታውቀው፡፡
የሀበሻ ቀጠሮ! የሀበሻ ቀጠሮ የምትሉት… እኔ  የሀበሻ፣ የፈረንጅ ብዬ ከልጅ ልጅ ለይቼ አውቃለሁ!
አንተ ባትለይም እኛ ሀበሾች ዩኒክ ስለሆንን…
ዩኒክ! ዩኒክ ነው ያልከው! ቃሉን ስትናገረው አታፍርም! ሰዓት አለማክበር ዩኒክነት ነው?
አያ ጊዜ ምን አዲስ ነገር አለው! ሰዓት አለማክበር በዚህ ዘመን አልተጀመረ፡፡ እኛ እኮ ሦስት ሺህ፣ አይደለም አምስት ሺህ ዘመን…
የቁጥር አባዜ የማይለቃችሁ እናንተን አየሁ፡፡ በሦስት ሺህ ዘመን ትኮራላችሁ…የበይ ተመልካች በሆናችሁበት የአፍሪካ ዋንጫ “ከሠላሳ አንድ ዓመት በኋላ…” እያላችሁ ትኮራላችሁ… እኔን ለምን መሸሸጊያ ታደርጉኛላችሁ?
አያ ጊዜ፣ እንዲህማ አፈር ድሜ አታስገባንም፡፡
የዛሬ አርባ ዓመት ኮሪያና ኢትዮጵያ ተመሳሳይ የዕድገት ደረጃ ላይ ነበሩ ትላላችሁ፡፡ እነሱ በደንብ ሲጠቀሙብኝ፣ እናንተ እንደ ገና ሩር ከአንድ ጫፍ አንድ ጫፍ ስትለጉኝ አይደል እንዴ የኖራችሁት! እኮ ንገረኛ… በአርባ ዓመት እነሱ እዚህ ደረጃ ሲደርሱ እናንተ የማንን ጎፈሬ ስታበጥሩ ነበር! ፋታ አጣና! ፋታ አጣን…እንደምታውቀው በእኛ የማይመቀኝ የለም…
ዓለም ሁሉ ነዋ በእናንተ ላይ የሚያሴር! እሺ ተመቀኟችሁ እንበል፤ እኔን በአግባቡ ካለመጠቀም ጋር ምን ያገናኘዋል! ለቁም ነገሩ ስትጎተቱ ለፍሬ ከርስኪው ነገር ማንም አይቀድማችሁም፡፡
አያ ጊዜ፣ ምን ማለትህ ነው?
ይሄኔ አንተ አንዷን ቆንጆ ብትቀጥር ኖሮ፣ እንኳን እንደ እኔ አንድ ሰዓት ልትገትራት፣ ለአራት ሰዓቱ ቀጠሮ ሁለት ሰዓት ሳይሞላ ሬስቱራንት፣ ወይ አውቶብስ ፌርማታ ትደርስ ነበር…
አያ ጊዜ፣ አንተ ደግሞ…ቅድሚያ የሚሰጣቸው ነገሮች አሉና!
እኔን አሰቃያችሁኛ! ወይ አንደኛውን ትቻችሁ ጓዜን ጠቅልዬ አልሄድ ታሳዝኑኛላችሁ፡፡ እስቲ ንገረኝ… ሁለት ሰዓት ተኩል ይጀመራል የተባለው ስብሰባ አራት ሰዓት እንኳን የማይጀመረው ለምንድነው?
የክብር እንግዳውስ አያ ጊዜ…የክብር እንግዳውስ! የክብር እንግዳው ሳይመጣማ ስብሰባ አይጀመርም፡፡
የእናንተ አገር ስብሰባ ያለ ክብር እንግዳ አይሆንም ነው የምትለኝ!
በጭራሽ! አይሆንም ሳይሆን አይታሰብም፡፡ አያ ጊዜ ለእኛም አስብልን እንጂ! አንተ ስታስበው የክብር እንግዳ የሌለው፣ መደረኩ በባንዲራ ያልተንቆጠቆጠ፣ በየሰዉ ፊት የታሸገ ውሀ ያልተቀመጠበት ስብሰባ ምኑን ስብሰባ ነው!
የክብር እንግዳ ባይኖርስ ሰማዩ ይደፋባችኋል?
ዜና አይነገርልንማ! አየህ፣ ስብሰባን ትኩረት እንዲያገኝ የሚያደርገው አጀንዳው ሳይሆን የክብር እንግዳው ማነው የሚለው ነው፡፡ አንተ ልጄ… ምን አለብህ…
እኮ በማንኛውም ስብሰባ የክብር እንግዳ መኖር አለበት የሚል ህግ አላችሁ እንዴ!
አልገባህም አያ ጊዜ፣ የክብር እንግዳ ከሌለ ዜናው አይነገርም እያልኩህ እኮ ነው፡፡ ደግሞ ዜና ያልተሠራበት ስብሰባ ዋጋ የለውም፡፡ እየው ዜናው እንኳ ሲጀምር እንዴት መሰለህ… “በንጽህና ያልተጠበቀ የመኖሪያ አካባቢ የጤና ችግሮችን እንደሚያስከትል አቶ እከሌ አስገነዘቡ” ብሎ ነው። ከዛም ይቀጥልና… “አቶ እከሌ ይህን የተናገሩት በክብር እንግድነት በተገኙበት በጤና ጉዳዮች ላይ በሚመክረው ጉባኤ ላይ ነው…” ይልና ሦስተኛው ዓረፍተ ነገር ምን ይል መሰለህ…“ጉባኤው በሚቀጥለው ሰኞ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ይጠናቀቃል…” አየህልኝ አይደል!
እሺ የክብር እንግዳውስ ምን ይጎትተዋል…በሰዓቱ አይመጣም!
ኸረ እባክህ ቀስ በል! ደግሞ ጦስ እንዳታመጣብኝ…እንደውም ሰሞኑን ዙሪያዬን የሚያንዣብበው በዝቷል፡፡
እኮ አስረዳኛ… የክብር እንግዳው ለምን በሰዓቱ አይመጣም?
በሰዓቱ ከመጣማ ምኑን የክብር እንግዳ ሆነው! ስማ አያ ጊዜ፣ በሰዓቱ አለመምጣቱ እኮ አንዱ የክብር እንግዳ መገለጫ ነው፡፡
እሺ የክብር እንግዳው ቶሎ ሲመጣ እንኳን ስብሰባ የማይጀመረው ለምንድነው?
ቴሌቪዥንስ! የቴሊቪዥን ካሜራ በሌለበት እንዴት ስብሰባ ይጀመራል! ንገረኝ ካልክ ብዙ ስብሰባዎች የሚደረጉት እኮ ለቴሊቪዥን ዜና ነው፡፡ እየው፣ ስማኝማ…እንኳን የክብር እንግዳ፣ ሙሽሮች እንኳን በሰዓቱ መምጣት ትተዋል፡፡ እንግዶቻቸውን በሰባት ሰዓት ጠርተው እኮ እነሱ በአሥር ሰዓት ነው የሚደርሱት፡፡ እንደውም ስልክ እየተደወለ ሰዉ ገና እየገባ ስለሆነ ቆይታችሁ ኑ ይባላሉ፡፡
የእነሱ ደግሞ ጭካኔ ነው፤ ሰዉን በባዶ ሆድ…
በባዶ ሆድ! አያ ጊዜ… ሰዉ ነቄ ሆኗል፡፡ ባዶ ሆዱን ሠርግ መሄድ እኮ ትቷል፡፡ ልጄ ጥስቅ አርጎ በልቶ ነው የሚመጣው፡፡
ደግሞ እኮ እኔን መጀመሪያውኑ በሚገባ ሳትጠቀሙብኝ በሆነ ባልሆነው “ተራዝሟል…” የምትሉት ነገር አላችሁ፡፡
አያ ጊዜ፣ አልገባኝም…
“ለምዝገባ ሠላሳ ቀን ተሰጥቷል…” ካላችሁ በኋላ ቆይታችሁ “ምዝገባው ለአሥራ አምስት ቀን ተራዝሟል…” ትላላችሁ፡፡ መጀመሪያ ከሠላሳ ቀኑ ሦስቱን እንኳን በስርአት ተጠቅማችሁ ቢሆን ጥሩ፡፡ አንገላታችሁኝ፣ ተጫወታችሁብኝ…
እኛ እኮ ጥፋት የለብንም፡፡
እንዴት ጥፋት የለባችሁም…
ገና ምዝገባው አንድ  ወር ሲባል ለአሥራ እምስት ቀን እንደሚራዘም እናውቃለና፡፡
ንቃችሁኛል፣ ደፍራችሁኛል፣ ቢታመንም ባይታመንም በቁሜ ቀብራችሁኛል፡፡
አያ ጊዜ፣ ፖለቲካ መናገር ጀመርክ እንዴ! ለነገሩ አንተን ማን ይነካሃል…እኔ ልጆቼን ላሳድግበት፡፡ እንደው ልጅ ስል ምን ትዝ አለኝ መሰለህ---ዘንድሮ ልጅ እንኳን የተባለበትን ጊዜ ጠብቆ መወለድ ትቷል፡፡ ይመጣል ከተባለበት ሦስት ሳምንት ቆይቶ ይመጣል…
ይሄ በዚህ ቀን ይመጣል የሚሉት ሀኪሞች ችሎታ ማነስ ነዋ!
አይደለም…አያ ጊዜ እንደ እሱ አይደለም፡፡ ሀኪሞቹ ምንም ችግር የለባቸውም፡፡ አየህ የዘንድሮ ልጅ ተንኮል የሚጀምረው ገና ሳይወለድ ነው…
ጀመረህ ደግሞ፣ ይህን በትውልድ ላይ ጣት መቀሰር ጀመርከኝ…
እውነቴ እኮ ነው…
እኔ የምለው እዚህ አገር መቼ ነው አንዱ ትውልድ በሌላው ላይ ጣት መቀሰሩን የሚያቆመው! ምነው ሌላው አገር እንዲህ አይናቆር!
አይደለም፣ ምን መሰለህ…
ግዴለም፣ ግዴለም ይበቃናል፡፡ የእናንተን ነገር ስናወራው ብንውልና ብናድር ለከርሞም አንጨርሰው፡፡  ወይ ጉድ…የአንተው አንሶ እያስለፈለፍከኝ እኔኑ እኮ ራሴን በራሴ እንዳጠፋ እያደረግኸኝ ነው! ደህና ሰንብት!
“ወይ ጊዜ፣ ወይ ጊዜ…” ከሚል አይነት እንጉርጉሮ አውጥቶ…አለ አይደል…‘ጊዜ’ንና እኛን የሚያዋድደንን ተአምር አንድዬ ይላክልንማ፡፡
ደህና ሰንበቱልኝማ!

Published in ባህል

    አዲስ አድማስ ጋዜጣ ቅዳሜ ሰኔ 13 ቀን 2007 ባወጣው እትሙ፤ “የአልፋ ባለአክሲዮኖችና አመራሮች እየተወዛገቡ ነው” በሚል ርዕስ ከአልፋ የትምህርትና ስልጠና አ.ማ ቦርድ ሰብሳቢ፣ የተሠጡትን የተሳሳቱና አደናጋሪ መረጃዎችን ማረም ተገቢ ይመስለኛል፡፡ በዚህም መሰረት ከትርፍ፣ ከተማሪ መቀነስና ከትምህርት እንዲሁም ከካፒታልና ከሕንፃ ግንባታ ጋር በተያያዘ አጭር በመረጃ ላይ የተደገፈ ግምገማ ለማቅረብ እሞክራለሁ፡፡  
በ2006 ዓ.ም የማህበሩ የተጣራ ትርፍ ተብሎ 4,679,586 ብር በሪፖርት ላይ ቢገለጽም 8 ሚሊዮን ብር የአያት ኩባንያ እዳ በስሌቱ ውስጥ ቢገባ ኖሮ፣ ይህን ያህል ትርፍ ሳይሆን ኪሳራ (loss) በቀረበ ነበር፡፡
እውነታው እንዲህ ቢሆንም የቦርዱ ሰብሳቢ፤ “ትርፍ በአስጊ ሁኔታ እየቀነሰ አይደለም፣ ቅነሳው አያሳስበንም፣ የኪሳራና የውድቀት ስጋት የለብንም፣የባለአክስዮኖች ቅሬታ በፊት ሲገኝ ከነበረው ትርፍ በመቀነሱ ነው” በማለት አለአግባብ በማጣጣልና በማናናቅ ተናግረዋል፡፡ ይኸም ችግሩን ለመደበቅ እና ለመሸፋፈን የታለመ ነው፡፡
ከቢዝነስ አንጻር አንድ የንግድ ተቋም ኢንቨስት ካደረገውና ሠርቶ ሊያገኘው ከሚገባው ወይም ካሰበው በታች ትርፍ ካገኘ ኪሳራ (loss) ደረሰ ይባላል፡፡ በዚህ መልኩ በአልፋ ላይ የደረሰው ኪሣራ በነበሩት ሕንፃዎች ካለ ኪራይ የነበሩትን የድርጅትና ሌሎች ሐብቶች በነፃ ተጠቅሞ የነበረውንም የቢዝነስ ዕድል ባለመጠቀሙ በመሆኑ ኪሣራው እጅግ የላቀ ይሆናል፡፡ መፍትሔም ስላልተገኘለት እጅግ ያሳስባል፡፡ በሌላ በኩል ተቋሙ በየጊዜው መክፈል ያለበትን እየከፈለና ስራውን እየሠራ መቀጠል ካቃተው ተንገራግጮ ቆሟል ማለት ነው። ይህም በንግድ ህጉ መሠረት ኪሳራ (bankruptcy) ሲባል፣ ኪሳራውም በፍርድ ቤት መታወጅ አለበት። በርግጥ አልፋ ሁለተኛውና የመጨረሻው ደረጃ ላይ አልደረሰም፤ ሆኖም በተለይ ሕጋዊ መጠባበቂያ ገንዘቡ ሕንፃ እየተገነባበት ስለሆነ ትንሽ ችግር እንኳን ቢፈጠር ለዚህ ዓይነት ኪሣራ ሊጋለጥ ይችላል፡፡ የባለአክሲዮኖቹ ትግልና ጭንቀት ወደዚያ እንዳይደርስና አጠቃላይ ውድቀት እንዳይከተል ነው፡፡ ባለፉት አመታት የታየው ሂደት ከቀጠለና በወሳኝ መልኩ ካልተቀለበሰ ደግሞ አይቀርለትም፡፡
በሌላ በኩል በአልፋ እጅግ አስደንጋጭ የተማሪ ቅነሳ የታየበት ቢሆንም ምንም ዓይነት መፍትሔ ካለመቀየሱም በላይ የቦርዱ ሰብሳቢ በቅነሳው አልተደናገጥንም ብለዋል፡፡ በዚህ ሁኔታ ያልተደናገጠ መሪ መፍትሔም ስለማይፈልግ ችግሩ እንዳለ ቀጥሏል፡፡ በዲግሪና በተለይም በ2ኛ ዲግሪ ደረጃ የፕሮግራሞቹን ሕልውና የሚፈታተኑ ችግሮች እንዳሉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ መደማመጥ ከተቻለ ችግሮቹንና መፍትሔዎችን ማቅረብ ይቻላል፡፡
ሰብሳቢው እንዳሉት፤ የርቀት ትምህርትን በተመለከተ የገበያ ድርሻው የቀነሰው በተፎካካሪዎች መበራከት ሳይሆን የኩባንያው አመራር በተሻለ ሁኔታ ተወዳዳሪ ሆኖ ከገበያው የሚገባውን ባለማግኘቱ ነው፡፡ በጥራቱም በኩል በተሻለ ሁኔታ ላይ ቢሆን ኖሮ በተማሪ ብዛት ይጨናነቅ ነበር እንጂ በተማሪ “ድርቅ” አይመታም ነበር፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ካፒታሉን ወደ 125 ሚሊዮን ብር አሳድገናል በማለት የቦርዱ ሰብሳቢ የተናገሩትን በተመለከተ፣ ካፒታሉ ያደገው በ1997 ዓ.ም ማለትም ከ11 ዓመታት በፊት ነው፡፡ የአልፋ ችግሮች የተከሰቱት በተለይም ከ2001 ዓ.ም በኋላ ነው፡፡ በነዚህ ዓመታት በስልጣን ላይ የነበሩት ቦርድና ማኔጅመንት ካፒታል የሚገነባ ስራ ባይሰሩም፣ ዘወትር የሚነግሩን ህንፃዎቹን እንደዘበኛ ጠብቀን በማቆየታችን አትከስሩም፣ እንዲያውም ሲሸጡ ትርፍ ታገኛላችሁ የሚል ነው፡፡ የባለአክሲዮኖቹ ክርክር ደግሞ ባለው ሀብት ሰርታችሁ ለደንበኛው አርኪ አገልግሎት፣ ለኛ ደሞ ጥቅም አላስገኛችሁም የሚል ነው፡ በሌላ በኩል ሰብሳቢው በተደጋጋሚ የገለጹት ነገር ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተለያዩ የግል ህንፃዎችንና ትምህርት ቤቶችን በየቦታው በመገንባት ቋሚ ንብረት እያፈራን ነው የሚል ነው፡፡ ነገር ግን እሳቸው እንዳሉት፤ በቅርብ ጊዜ ት/ቤቶችና ሕንፃዎች በትርፍ እየተገነቡ አይደለም፡፡ በሌላ በኩል የአልፋ ችግሮች፣ መንስኤዎችና መፍትሔዎች በሕንፃ ላይ የተመሠረቱ አይደሉም፡፡ ችግሩ ያሉትንም ሐብቶች ወደ ውጤት ለመቀየር አለመቻል ነው፡፡ እዚህ ላይ ዋናው ጉዳይ ከአመራር ድክመት የተነሣ፣ ተቋሙና ቢዝነሱ ለመሥራት አለመቻላቸው ነው፡፡
አልፋ በሥራውና በውጤቱ ማሽቆልቆል ከጀመረበት ጊዜ በተለይም ከ2003 ዓ.ም አንስቶ  ባለአክሲዮኖች ባለማሰለስ ችግሮችንና የመፍትሔ ሃሳቦችን አቅርበዋል። እንዲሁም ከ2005 ጀምሮ ከባለአክሲዮኑ 10% በማስፈረም፣ ችግሮችንና መፍትሔዎችን እንዲሁም የመመስረቻ ጽሑፍና የመተዳደሪያ ደንቡን ለማሻሻል የሚያስችል የመነሻ ሃሳብ ቢያዘጋጁም በወቅቱ በነበረው ቦርድ ሐሳቦቹ ለጠቅላላ ጉባኤ ቀርበው ውይይት እንዳይደረግባቸው ሆነዋል፡፡ በዚህም የተነሳ ኩባንያችን እነሆ ዋጋ ለመክፈል ተገዷል፡፡ ችግሮቹንና መፍትሔዎችን መደበቅና መሸፋፈን ከቀጠለ ገና ብዙ ሊያስከፍል ይችላል። በጠቅላላ ጉባዔ የባለአክሲዮኖች አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት ባቀረቡት ችግሮች ላይ የምርመራ ኦዲት እንዲሠራ ቢወሰንም፣ በወቅቱ የነበረው ቦርድ ውሳኔውን ወደ ማኔጅመንት ኦዲት ቀይሮት እሱም ተኮላሽቶ እንዲቀርብ አድርጐታል፡፡ በዚሁ በተኮላሸው የማኔጅመንት ኦዲት ውጤት ላይ ለመወያየት ታህሳስ 26 ቀን 2007 ዓ.ም በጉባዔው ላይ በባለአክሲዮኖች ተጠይቆ ስምምነት ላይ በተደረሰው መሠረት፣ የአልፋ ችግሮችና መፍትሔዎች ላይ የሚወያይ ጠቅላላ ጉባዔ በቅርቡ ተጠርቶ፣አልፋ ከተቻለ ወደ ሃዲዱ እንዲመለስ፤ ካልተቻለም የተሻለ ውሳኔ ቢወሰን ለሁሉም ይበጃል። በሽታውን የደበቀ በተዓምር መድሃኒት ሊገኝለት አይችልም፡፡  

Published in ህብረተሰብ

ከ800 በላይ ሰዎች ተመራቂዎቹን ለመቅጠር ተመዝግበው ይጠባበቃሉ
- የሰለጠኑ ሞግዚቶች የሙያ ምዘና ብቃት ፈተና (coc) ይወስዳሉ
- ከማዕከሉ የተመረቁ ሞግዚቶች በ1500 ብር መነሻ ደሞዝ ይቀጠራሉ

     በሰለጠነው ዓለም የህፃናት አያያዝና አስተዳደግ ራሱን የቻለ ሳይንስ ሆኖ በከፍተኛ ደረጃ ትምህርት የሚሰጥበት ሙያ ነው፡፡ ትውልድን በጥሩ ሥነ ምግባር ቀርፆና አንፆ ለማሳደግ ለሚያስችለው ለዚህ ትልቅ ኃላፊነት ለመታጨት ሥነ - ልቦናዊ ዝግጅት በእጅጉ ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ ህፃናት ጤናቸው በአግባቡ ተጠብቆ፣ በአካልና በአዕምሮ ዳብረው፣ በሥነ ምግባር ታንፀው እንዲያድጉ አሳዳጊዎቻቸው ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያደርጋሉ።
እዚህ አገራችን ይህ የህፃናት እንክብካቤና አያያዝ ሙያ ልዩ ስልጠናና ዕውቀት የሚያስፈልገው መሆኑ እንኳን እምብዛም በማይታወቅበት ሁኔታ የህፃናት አያያዝ፣ አስተዳደግና እንክብካቤ ላይ የንድፈ ሃሳብና የተግባር ስልጠና በመስጠት፣ አሰልጥኖና የሙያ ብቃት ምዘናን አስፈትኖ በብቃት እያስመረቀ ሥራ የሚያስቀጥር አንድ ተቋም መኖሩን ሰማንና ወደዚያው አመራን፡፡
እሹሩሩ የሞግዚቶች ማሰልጠኛ የሚል ስያሜ የተሰጠውን የስልጠና ማዕከል ጎብኝተን፣ ለማዕከሉ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ለአቶ ሰለሞን ሙሉጌታ ስለ ተቋሙ አመሰራረትና ስለ ስልጠናው አጠቃላይ ሁኔታ አጭር ቃለ ምልልስ አደረግንላቸው፡፡
ማዕከሉን ለመመስረት ሃሳቡ እንዴት መጣ?
ይህንን የስልጠና ማዕከል ለመክፈት የቻልነው በራሳችን በቤታችን ላይ በደረሰ አጋጣሚ ተነስተን ነው፡፡ የመጀመሪያ ልጃችንን እንደወለድን፣ ያው እንደ አብዛኛው ሰው የህይወት ሩጫችንን ለመሮጥ ልጃችንን ለሞግዚት ሰጥተን ከቤት ወጣን፡፡ ከቀናት በኋላ ልጃችን ላይ አዳዲስ ባህርያትን ማስተዋል ጀመርን፡፡ ከዚህም ሌላ ልጃችን ሞግዚቷ የምትናገረውን ቋንቋ መልመዱ ደስታን ቢሰጠንም፣እንዴት ሊለምድ ቻለ የሚለው ነገር በጣም አሳሰበን፡፡ በተጨማሪም ከሞግዚቷ የወረሳቸው አንዳንድ ባህሪያት ሁኔታውን ትኩረት ሰጥተን ማየት እንዳለብን የሚያስገነዝቡ ነበሩ፡፡ ልጁ እናቱንም አባቱንም እየመሰለ አልሄደም፡፡ ሁኔታው ትንሽ አስደንጋጭ ነበር፡፡
በመጀመሪያ ያደረግነው ነገር በልጅቷ ላይ የምናያቸው ትክክል ያልሆኑ ባህርያትን እንድታስተካክል ማድረግ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ችግሩ በእኛ ቤት ብቻ ያለመሆኑንና የዚህ ዓይነት ችግር ሲያጋጥም መፍትሄ ሊያስገኝ የሚችል ተቋም መኖር አለመኖሩን ለማጥናት ሙከራ አደረግን፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ ያየነው እውነታ፣ ህፃናት በቤታቸው ውስጥ በቅርበት በሚያዩዋቸው ነገሮች እንደሚቀረፁ ነው፡፡ የሞግዚቶቻቸውን ቋንቋ እና ባህርያት ወርሰው እንዳገኘናቸው ልጆች ሁሉ፣ ቤት ውስጥ ቲቪ በየዕለቱ በማየት፣ በአረብ ቻናል ቲቪ ተቀርጸው አረብኛ ሁሉ መናገር የሚችሉ ልጆች ገጥመውናል፡፡
ጉዳዩን ስንመለከተው ክፍተቱ በጣም ሰፊ ነው። የተወሰኑ ጥያቄዎችን አዘጋጅተን በህፃናት መዋያ፣ በዴይኬር፣ በህፃናት ማሳደጊያዎች ውስጥ እየተዘዋወርን መጠየቅ ጀመርን፡፡ በአብዛኛዎቹ (በሁሉም ማለት ይቻላል) ውስጥ ያገኘናቸው የህፃናቱ ተንከባካቢ በመሆን የተቀጠሩት ሠራተኞች ስራቸውን እንደማይወዱት፣ በደመወዛቸው ደስተኛ እንዳልሆኑ፣ ሳይንሳዊ የሆነ የልጅ አያያዝ፣ አስተዳደግና ቅጣት የማያውቁ እንደሆኑ ተረዳን። በቤታችን ውስጥ የመጀመሪያውና ትልቅ ለውጥ ያገኘንበት ሁኔታ አበረታታንና ስራውን ለመስራት ውሳኔ ላይ ደረስን፡፡ ለአንድ ዓመት ያህል ጉዳዩን ስናጠናና ስንዘጋጅ ቆይተን፣ በ2005 ዓ.ም መስከረም ወር ላይ ማዕከሉን ከባለቤቴ ከወ/ሮ ምህረት አበራ ጋር አቋቋምነው፡፡
ሥራውን ስትጀምሩ ከሰዎች ምን አስተያየት አገኛችሁ?  ስራው በህብረተሰቡ ዘንድ ተቀባይነትን ያገኝልናል የሚል እምነት ነበራችሁ?
ስልጠና መስጠቱን ስንጀምር ምን እየሰራህ ነው ብለው የተገረሙብኝ ብዙዎች ነበሩ፡፡ እንዴት ይህንን ስራ ብለህ ታስባለህ፣ ማንም ሊቀበልህ አይችልም ሁሉ ብለውኝ ነበር፡፡ እኛ ግን እርግጠኛ ነበርን፡፡ አሁን ያለንበት ጊዜ የሩጫና የሥራ ነው፡፡ በርካታ እናቶች ልጆቻቸውን ለሞግዚት በመስጠት የህይወት ሩጫቸውን ለመሮጥ ከቤታቸው መውጣታቸው እየተለመደ ነው፡፡ በዚህ ምክንያትም ልጆች የሚያድጉት በሞግዚቶቻቸው እጅ ነው፡፡ ያቺ ልጅ አሳዳጊ ሞግዚት ደግሞ ስለ ልጅ አያያዝና አስተዳደግ በቂ ዕውቀትና ግንዛቤ ያላትና ልጆችን የምትወድ መሆን ይኖርባታል፡፡ ይህቺን ሞግዚት አሰልጥኖ ለሥራ የሚያዘጋጅ ተቋም ማቋቋሙ ምንግዜም ቢሆን ተቀባይነት ማግኘቱ የማይቀር ነው፡፡ በዚህ እምነት ነበረን፡፡
ከዚህ በተጨማሪም በቤታችን ውስጥ ባለችው የልጃችን ሞግዚት ላይ ያገኘነው ለውጥ ትልቅ ብርታት ሰጠን እናም ቀደም ሲል እንሰራቸው የነበሩትን ስራዎች ሁሉ ትተን ሙሉ ጊዜያችንን ለስልጠና ማዕከሉ ሰጥተን ስራችንን ቀጠልን፡፡ ቀስ በቀስ ሰልጣኞች እየመጡ መመዝገብና መሰልጠን ጀመሩ፡፡ በመቀጠልም የሰለጠኑ ሞግዚቶችን ለመቅጠር የሚፈልጉ ግለሰቦችና ተቋማት መምጣት ጀመሩ፡፡
 የምትሰጡት ምን ዓይነት ስልጠና ነው? ለምን ያህል ጊዜስ ነው የሚሰለጥኑት?
በማዕከላችን ለስልጠና የሚመጡት ሰልጣኞች የሚያገኙት የቲኦሪና የተግባር ትምህርት ነው፡፡ ቲኦሪው 20%፣ ተግባሩ 80% የሚሆን ድርሻ አለው፡፡ ስልጠናው የሚጀመረው ሰልጣኞቹ ስለ ግል ንፅህና አጠባበቅ፣ ስለ ህፃናት አያያዝና አስተዳደግ አጠቃላይ የቲኦሪ ትምህርት በመስጠት ነው፡፡ ከዚያ በመቀጠል በቲኦሪ የተማሩትን በተግባር የሚያጠኑበትና የሚለማመዱበት ራሱን የቻለ ለህፃናት አስተዳደግ የሚያስፈልጉ ነገሮችን በሙሉ ያሟላ ማዕከል ውስጥ የተግባር ስልጠና እንዲያገኙ ይደረጋል። የህፃናት አያያዝ፣ አልባሳትና ዳይፐር መቀየር፣ ህፃኑን መንከባከብ፣ ህፃናትን ማጠብ፣ ንፅህናቸውን መጠበቅ፣ ማስተኛት፣ ማጥባት ማቀፍ፣ ምግብ መመገብ፣ የልብስ ንፅህና አጠባበቅ፣ የህፃናት ምግብ አዘገጃጀት ሁሉ ይማራሉ፡፡ ለዚህ ተብለው የተዘጋጁና በውድ ዋጋ ከውጭ አገር ያስመጣናቸው መጥባትና መፀዳዳት የሚችሉ አሻንጉሊቶች አሉን፡፡ ትምህርቱ የሚሰጠውም በእነዚህ አሻንጉሊቶች ነው፡፡ ህፃናቱ በድንገት ቢታመሙባቸው ምን ዓይነት እርምጃ መውሰድ እንደሚገባቸው፣ በህፃናቱ ላይ የሚስተዋሉ ለውጦችን እያዩ አፋጣኝ እርምጃ መውሰድ የሚቻልበትን መንገድ መፈለግ፣ ልጆች ዳይፐር እንዲያቆሙ እንዴት ማድረግ ይቻላል፣ የልጆች ምግብን ከብክነት መከላከል የሚቻልበት መንገድ እንዴት ነው ---- የሚሉ ነገሮችን ሁሉ እናስተምራለን፡፡
የስልጠና ጊዜያችን በሁለት ይከፈላል፡- አንዱ የአንድ ወር ከአስራ አምስት ቀን ሲሆን ስልጠናው በሣምንት ለስድስት ቀናት የሚሰጥ ይሆናል፡፡ ሁለተኛው የሶስት ወራት ስልጠና ነው፡፡ በሳምንት 3 ቀን ሰልጣኞቹ በመረጡበት ጊዜ የሚሰጥ ነው፡፡
ለስልጠና የሚመጡ ሰልጣኞችን የምትመርጡበት መስፈርት አላችሁ?
አለን፡፡ ለምዝገባ የሚመጡ ሰልጣኞችን የምንቀበልበት መስፈርት አለን፡፡ ከሁሉም የምናስቀድመው ግን የሰልጣኛችንን ባህርይ ነው። ከልጆች ጋር የመሆን ፍላጐት እንዳላት፣ ኃላፊነት የሚሰማት እንደሆነች ሁሉ በሚገባ እናያለን፡፡
አንዳንድ የባህርይ ችግሮች ካሉ፣ ባሉን የስነልቡና ባለሙያዎች በመታገዝ ወደ ትክክለኛው መንገድ እንዲመጡ እናደርጋቸዋለን፡፡ ይህ ካልሆነም ከስልጠናው ይሰናበታሉ፡፡ ምክንያቱም ሰልጣኞቻችን ተመርቀው ሥራ ሲጀምሩ እንደ ሌላ ሙያ የሚገናኙት ከኮምፒዩተር፣ ከማሽንና ከወረቀት ጋር አይደለም፡፡ ከፍተኛ ጥንቃቄና እንክብካቤን ከሚፈልጉ ህፃናት ጋር ነው፡፡ ስለዚህም ትልቅ ጥንቃቄን የሚፈልግ ሥራ ነው፡፡
ሰልጣኞቹ ለሙያው ብቁ ናቸው ተብለው ለሥራ ዝግጁ የሚሆኑት መቼ ነው?
የቲኦሪና የተግባር ትምህርቱን ያጠናቅቃሉ። የቡድን ሥራዎቻቸውን ይሠራሉ፣ የመመረቂያ ጽሑፎች ያዘጋጃሉ፡፡ አፓረንትሺፕ ይወጣሉ፡፡ ይህንን ከአጠናቀቁ በኋላ ከአዲስ አበባ ፖሊስ፣ ከሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ እና ከ IOM ጋር በመተባበር ከወንጀል መከላከል የሚችሉበትን መንገድ አስመልክቶ ስልጠና ይሰጣቸዋል። ይህንን ሲያጠናቅቁም በሙያ ብቃት ምዘና ኤጀንሲ የሚሰጠውን የሙያ ምዘና ብቃት ፈተና (COC) እንዲወስዱ እናደርጋለን፡፡
በዚህ መልኩ ያሰለጠናቸውን 75 ሞግዚቶች፣ በቅርቡ በሳሮማሪያ ሆቴል በተደረገ ሥነስርዓት አስመርቀናል፡፡ ይህም በአገሪቱ የሙያ ምዘና ብቃት ማረጋገጫ የወሰዱ ሞግዚቶችን ለመጀመሪያ ጊዜ አሰልጥኖ ያስመረቀ ማዕከል እንድንሆን አድርጐናል፡፡
እስከ አሁን በአጠቃላይ ምን ያህል ሰልጣኞችን አሰልጥናችሁ አስቀጠራችሁ?
እስከ አሁን ወደ 265 የሚሆኑ ሞግዚቶችን አሰልጥነን ሥራ አስቀጥረናል፡፡ እነዚህ መቀጠር የሚፈልጉት ናቸው። ከዚህ ውጪ በተለያዩ ምክንያቶች መቀጠር የማይፈልጉ (የራሳቸውን የልጆች ማቆያና መንከባከቢያ) መክፈት የሚፈልጉ፣ በሥራ ላይ ያሉ፣ ወደ ውጪ አገር ለመሄድ የሚሹ ሁሉ ስልጠናውን ይወስዳሉ፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሰርተፍኬታቸውን አረጋግጦላቸው፣ ወደ ካናዳና አሜሪካ የሄዱ ሞግዚቶችም አሉን፡፡ ከዚህ ውጪ ያሉና ሥራ ለመቀጠር ፈልገው የሰለጠኑ ሞግዚቶቻችንን መነሻ ደመወዝ ከ1500 ብር በላይ በማድረግ በተለያዩ የግለሰብ ቤቶችና ተቋማት እንዲቀጠሩ አድርገናል፡፡ በ1500 ብር መነሻ ደመወዝ ተቀጥረው ዛሬ ደመወዛቸው ከ2500 ብር በላይ የሆነላቸው ሞግዚቶችም አሉን፡፡ ሰልጣኞቻችን ስልጠናውን ሲጨርሱ የመቀጠር ሥጋት አይኖርባቸውም፡፡
ገና ስልጠናውን በጨረሱ ሣምንት ከ1500 ብር በላይ ደመወዝተኛ ሆነው እንደሚቀጠሩ እርግጠኞች ነን፡፡ ሠልጣኞቻችን ስልጠናውን ሲያጠናቅቁ፣ ወስደው ለመቅጠር ተመዝግበው የሚጠባበቁ ከ800 በላይ ቀጣሪዎች አሉ፡፡
ከቀጣሪዎችና ከተቀጣሪዎቹ ኮሚሽን ትቀበላላችሁ?
ከቀጣሪዎቹ ኮሚሽን እንቀበላለን፡፡ ተቀጣሪዎቹ ግን የራሳችን ስለሆኑ እነሱ የሚከፍሉት ኮሚሽን የለም፡፡
ለስልጠናው ምን ያህል ክፍያ ይጠየቃል?
አንድ ሰልጣኝ ለስልጠና የሚያስፈልጉትን ነገሮች በሙሉ አጠቃሎ ከ3-4 ሺህ ብር የሚደርስ ወጪ ያስፈልገዋል፡፡ ኮርሱን በጨረሱ ማግስት መነሻ የ1500 ብር ደመወዝተኛ ይሆናሉ፡፡ ሥራ የማግኘቱ ዕድል ሰፊ ነው፡፡
ሥራ የማስቀጠር ፈቃድ አላችሁ?
የእኛ ሥራ ጐን ለጐን መሄድ የሚችል ሥራ ነው፡፡ ሙያተኛን አሰልጥኖና አብቅቶ መልቀቅ ሳይሆን የሰለጠነውን ኃይል መጠቀም ለሚገባው ሰው መስጠቱ ተገቢ ነው ብለን እናምናለን፡፡ እናም ከአዲስ አበባ ሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ህጋዊ የማስቀጠር ፈቃድ ተሰጥቶናል፡፡ ሰልጣኞቻችንን በበቂ ሁኔታ አሰልጥነን፣ከቀጣሪዎቻቸው ጋር ህጋዊ ውል እንዲፈራረሙ እያደረግን እናስቀጥራለን፡፡
 የሰልጣኞቻችሁ የቀለም ትምህርት ደረጃስ እምን ድረስ ነው?
ከአራተኛ ክፍል ተማሪ እስከ ሁለተኛ ድግሪ ያላቸውን ተቀብለን አሰልጥነናል፡፡ ዕድሜያቸው ከ20-53 ዓመት የሚሆናቸውን ተቀብለን አሰልጥነናል፡፡
በማዕከሉ የሚሰለጥኑት ሴቶች ብቻ ናቸው?
እስከ አሁን ሁለት ወንድ ሰልጣኞችን ተቀብለናል፡፡ እኔ ይህ ነገር በጣም መለመድ ያለበት ጉዳይ ይመስለኛል። አባቶችም መሰልጠን አለባቸው፡፡ እናት ስትወልድ ከምጡና ከአስጨናቂው ጊዜ በኋላም ህፃኑን የመንከባከብ ኃላፊነት የሚወድቀው በእሷ ላይ ነው፡፡ አባት ለማገዝ ቢፈልግ እንኳን ይፈራል፡፡ ስልጠናውን ወስዶ ቢሆን ግን ይህ ችግር አይኖርም፡፡ ኃላፊነቱን ለመወጣት ይችላል። የወንድ ሰልጣኞችን ወደ ማዕከላችን መምጣት በጣም የምናበረታታው ጉዳይ ነው፡፡
 ምሩቃን ሞግዚቶችን ለመቅጠር ተመዝግበው የሚጠባበቁ 800 ሰዎች ጉዳይ በምን ያህል ጊዜ ይደርሳቸዋል?
እኛ አሁንም ሥራችንን እየሠራን ነው፡፡ ከሥር ከሥር እየመጡ የሚመዘገቡ ሰዎች አሉ፡፡ አሁን ለቀጣሪዎች የምንሰጠው የሶስት ወር ቀጠሮ ነው፡፡ ይህንን ረዥም ጥበቃ ለማስቀረት አሁን ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረግን ነው፡፡ አሁን ባለን ሁኔታ አስጨናቂ ነገሮች ከሌሉ የምንሰጠው የሶስት ወር ቀጠሮ ነው፡፡
አስጨናቂ ነገሮች ሲባል?
አንዳንድ ጊዜ ድንገተኛ ሁኔታዎች ሲከሰቱ ቅድሚያ የምንሰጥበት ሁኔታ አለ፡፡ ለምሣሌ እናት በህይወት ከሌለችና መሰል ችግሮች ሲከሰቱ አፋጣኝ ምላሽ መስጠት ይኖርብናል፡፡  
ህብረተሰቡ የሰለጠኑ ሞግዚቶችን ጠቀሜታ በሚገባ እንዲገነዘብ ምን መደረግ አለበት ትላላችሁ?
የሰለጠኑ ሞግዚቶች በሁሉም ህፃናት ባሉበት ሥፍራ ሁሉ ያስፈልጋሉ የሚል እምነት ቢኖረንም ከመኖሪያ ቤት በበለጠ በዴይኬሮች፣ በመዋዕለ ህፃናትና በህፃናት ማሳደጊያ ውስጥ መኖራቸው እጅግ ወሳኝ ጉዳይ ነው። ወላጆች ልጆቻቸውን ወደ ህፃናት መዋያ ሲያስገቡ የሚያዩት የግቢውን ንፁህ መሆን፣ የዕቃዎቹን መሟላት እንጂ በተቋሙ ውስጥ ያሉ ሙያተኞች በልጆች እንክብካቤ ላይ ያላቸውን ሙያዊ ብቃት አይደለም። ተቋማቱም ለቀጣዩ ዓመት ህንፃዎቻቸውን ከማደስ፣ አዳዲስ ዕቃዎችን ከማስገባቱ ጐን ለጐን በተቋሞቻቸው ውስጥ ያሉ ሙያተኞችን አቅም በማጐልበቱና ሙያዊ ስልጠና እንዲያገኙ በማድረጉ በኩል ቢተጉ ትልቅ ጠቀሜታ አለው፡፡
የወደፊት ዕቅዳችሁ ምንድነው?
አሁን ማዕከሉን አጠናክረን ከፍተኛ ቁጥር ያለውን የሰለጠኑ ሞግዚቶች ጥያቄ ለመመለስ ጥረት ማድረግ ነው ዓላማችን፡፡ ከዚህ በመቀጠልም ሌሎች ያሰብናቸውና በወረቀት ደረጃ ተሠርተው ያለቁ ፕሮጀክቶች አሉን። እንደየሁኔታው እነሱንም ተግባራዊ ማድረግ እንጀምራለን። አቅመ ደካማ ሰልጣኞችን በነፃ ማሰልጠን ቀደም ሲል እናደርገው የነበረና አሁንም የምንቀጥለው ተግባር ነው፡፡ አሁን ባለንበት ሁኔታ ማዕከላችንን እያስፋፋን፣ሰልጣኞችን በበቂ ሁኔታ ተቀብለን በማሰልጠን፣ ብቁ ሙያተኛ ማድረግና ራሳቸውን ማስቻል እንፈልጋለን፡፡

Published in ዋናው ጤና

ከዕለታት አንድ ቀን በደጋው አገር የሚኖሩ ሁለት ጐረቤታም ገበሬዎች ነበሩ። ሁለቱም በሣር ቤት የሚኖሩና ኑሮ አልለወጥ ያላቸው ግን ታታሪ ሰዎች ነበሩ፡፡
“አንድ ቀን አንደኛው በድንገት የኑሮ ለውጥ አሳየ፡፡ የግቢውን አጥር አጠረ። የቤቱን የሣር ክዳን ወደ ቆርቆሮ ጣራ ለወጠ፡፡ ልጆቹ ደህና ደህና ይመገቡ፣ መልካም ልብስም ይለብሱ ጀመር፡፡
ጐረቤትየው ያየውን ለውጥ ማመን አቅቶት ወደ ወዳጁ ሄደና፤
“አያ እገሌ?” አለው፡፡
“አቤት” አለው፡፡
አብረን አንድ አካባቢ እያረስን እየኖርን በድንገት ምን ተዓምር ተፈጥሮ ነው እንዲህ የበለፀግከው?”
የተለወጠው ገበሬም፤
“ሚሥጥሩ ምን መሰለህ ወዳጄ፤ ታች ቆላ ወርጄ ማጭድ፣ ዶማ፣ አካፋ፣ ማረሻ ወዘተ ብዙ ብረታ ብረት ገዝቼ አመጣሁና ለደገኛው ገበሬ ቸበቸብኩት። ትርፉ ትርፍ እንዳይመስልህ! አንድ ሁለት ሶስቴ ተመላልሼ ይሄንን ሥራ ስሠራ ገንዘብ እንደ ጉድ እጄ ገባ!” አለው፡፡
ያም ገበሬ አመስግኖት ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ በነጋታው፤ በሬዎቹን ሸጠና ብሩን ይዞ ወደ ቆላ ገበያ ወረደ፡፡ ቆላ ያለ የብረታ ብረት ዘር አንድም ሳይቀረው ገዛና ተሸክሞ ወደ ደጋ ሊመለስ መንገድ ጀመረ፡፡ መንገዱ ወደ ቆላ ሲሄድ ቁልቁለት ነበረ፡፡ አሁን ግን ዳገት ነው፡፡
ግማሽ መንገድ እንኳ ሳይጓዝ በሸክሙ ብዛት ወገቡ ሊቆመጥ ደረሰ፡፡ መቀጠል አልቻለም፡፡ ተዝለፍልፎ፣ ላብ በላብ ሆኖ ወደቀ፡፡
መንገደኛ የሰፈሩ ሰው ወድቆ አየውና፤
“አያ እንቶኔ?”
“አቤት”
“ምነው ምን ገጠመህ?”
“ኧረ ተወኝ ወዳጄ፤ ያ ጐረቤቴ ስለ ብረታ ብረት ንግድ አማክሮኝ፣ እዚህ ወድቄ ቀረሁልህ፡፡”
“እንዴት?”
“ትርፉን ነግሮ መከራውን ሳይነግረኝ!”
*   *   *
በህይወት ውስጥ፣ ደረጃው ይለያይ እንጂ መስዋዕትነትን የማይጠይቅ ምንም ነገር የለም፡፡ ይህንን ልብ ያላለ ፖለቲከኛ ብዙ ዕድሜ አይኖረውም፡፡ በትንሽ በትልቁ ሲበሳጭ፣ ሲነጫነጭ፣ አቤቱታ ሲያበዛ፣ ነገረ ሥራው ሁሉ የዕድል እንጂ የትግል ሳይመስል፣ ማማረር እንጂ መማር ሳይዳዳው፤ በአጭር ይቀጫል፡፡ በዱሮ ጊዜ “ትግላችን እረዥም፣ ጉዟችን መራራ” የሚል መፈክር ነበር፡፡ ጣፋጭና አጭር ትግል የለም ለማለት ነው፡፡ ትግል ጠመዝማዛ እንጂ ቀጥ ያለ መስመር እንደሌለው የሚያፀኸይ ጭምር ነው፡፡ በታሪክ ዕውነተኛ ትግል ያካሄዱ የዓለም ድርጅቶች ወይም የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚያስተምሩን ይሄንን ነው፡፡ ሳይታክቱ መታገል፣ ሽንፈትን በፀጋ መቀበል፣ ጉድለትን መመርመር ለቀጣዮቹ ዓመታት፣ ከአሁኑ መዘጋጀት! ዕቅድን እጥጉ ድረስ ማቀድና የትላንቱን እንቅፋት እስከመጨረሻው ማጽዳት ተገቢ ነው፡፡ ባላንጣን አለመናቅና እስከፍፃሜው መገላገል ተገቢው የጉዞው ፋይዳ ነው፡፡ ይሄንን ሳንገነዘብ ትግሉ ውስጥ ከገባን ፀፀት ማትረፋችን አይቀሬ ነው፡፡ ሮበርት ብራውን የተባለ ፀሐፊ እንዲህ ይለናል፡-
“ከሙሴ ጀምሮ የኖሩ ታላላቅ መሪዎች የፈሩትን ጠላት ሙሉ በሙሉ መደምሰስ እንዳለባቸው ያውቃሉ፡፡ (ይህንን የተማሩት በከባድ መንገድ ይሆናል አንዳንዴ) ከተዳፈነ እሳት ውስጥ አንዲት ፍም ካለች ምንም ደብዛዛ ብትሆን ቀስ በቀስ እሳት ማስነሳቷ አይቀሬ ነው፡፡ ግማሽ መንገድ ሄዶ ማቆም ከጠቅላላ ማጥፋት የበለጠ ኪሣራ ላይ ሊጥለን ይችላል፡፡ ጠላት አገግሞ ሊበቀል ይችላል። ስለዚህ በአካልም፣ በመንፈስም ማድቀቅ ያስፈልጋል”
ግማሽ መንገድ ተጉዞ መቆምን የመሰለ አደጋ የለም፡፡ “የነብርን ጅራት አይይዙም፤ ከያዙም አይለቁም” የሚለውን የአበሻ ተረት በጽኑ ማስተዋል ብልህነት ነው፡፡
ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፤
“…የተወጋ በቅቶት ቢኛ፣ የወጋ መች እንቅልፍ አለው፤
የጅምሩን ሳይጨርሰው፡፡” የሚለን ይሄንኑ ነው፡፡
ገና በጠዋት መንገድ ስንጀምር ትርፉን ሲነግሩን መከራውንም አብረን ማስታወስ፣ ትግልን ስናስብ መስዋዕትነትን አብረን ማሰላሰል፤ እጅግ ወሳኝ መሆኑን ከልባችን እናጢን፡፡ አለበለዚያ “መሳም አምሮሽ፣ ጢም ጠልተሽ” እንዲሉ ይሆናል!!

Published in ርዕሰ አንቀፅ
Page 11 of 17