በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነትና በፆረና ተጋድሎ እውነተኛ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥነው “የኢትዮ - ኤርትራ ጦርነትና የፆረና ተጋድሎ” የተሰኘ መፅሀፍ በትላንትናው እለት በሂልተን ሆቴል ተመርቋል፡፡ በምክትል አስር አለቃ የማታወርቅ ተገኝ ተፅፎ በዳዕሮ አድቨርታይዚንግ የተዘጋጀው ይህ መፅሀፍ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት የተከሰቱ ተጋድላችን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል ተብሏል፡፡
በምረቃ ሥነስርአቱ ላይ የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት፣ የጦር መኮንኖች፣ የታሪክ ምሁራንና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተው ነበር፡፡  

Saturday, 12 July 2014 12:37

ዳይኖሰር

የተከራየሁበት ቤት ልጅ ደመቀ ወደ ግሮሠሪዋ ገባ፡፡
ደመወዝ የምቀበልበትን ቀን አሥልቶ፣ እንደ ልክስክስ ውሻ አነፍንፎ የትም ልግባ ከች! ይላል፡፡ እናም አምስት ደብል ጂን የመጋበዝ ያልተፃፈ ሕግ ያስገድደኛል፡፡ ለምን? ደመቀ የአርባ ቀን እድሉ በዝቅጠትና ስካር የተጠቃለለ የሠፈር አውደልዳይ ነው፡፡
ከጐኔ ተቀመጠ፡፡ የጐን ውጋት፡፡ ደብል ጂን አዘዘ - አንገት ማስገቢያ፡፡ እንጥፍጣፊ ሳያስቀር ጨለጠ፡፡ እርቃኗን ቀርታ በባዶነት የምታዛጋውን መለኪያውን ትክ ብሎ አፈጠጠባት - በመቀጠል እኔን፡፡ እንደ ዱርዬ ድመት እየተቁለጨለጨ “ሚያው ጂን” ማለት ለቀረው ደመቀ ደብል ጂን አዘዝኩ - ለእኔም፡፡
“ምስኪን ፍጡር ነኝ” ሲል ጀመረ፤ እንደተለመደው
“ከሕይወት አገኘሁ የምለው ብቸኛው በጐ ነገር ከብሌን ጋር ያሳለፍኩት ንጹህ ፍቅርን ነው…ነበር…እህህ…”
ከብሌን ጋር ለተወሰነ ጊዜ አብረው ያሳለፉ መሠለኝ፡፡ አጠገቤ ዝር እንዳትል ብላ ካንባረቀችበት ግፋ ቢል አምስት ዓመት ቢያልፈው ነው፡፡ ጊዜው ረዘመ ቢያስብልም ከደመቀ እድሜ አንፃር (47) አምስት አመት ምን አላት፡፡ አንድ ቀን የግሉ እንደምትሆን ወደ ቅዠት ያደላ ህልም አለው፡፡
“ግን ጥቂት እንከኖቼን አልወደደችልኝም…ከጠዋት እስከ ውድቅት መጨለጤን -ጢምቢራዬ ዞሮ በየቦዩ ሥር መጋደሜ - ዘባተሎ አለባበሴ …ከሥራ አጥነቴ ጋር ተደማምሮ…እነዚህ ኢምንት ቅንጣት እንከኖቼ…እናም በስካር መንፈስ ተገፋፍቼ የፈፀምኩት ተራ ሌብነት ብሌን ጆሮ ሳይደርስ አልቀረም፡፡” ብሎ በሐፍረት አቀረቀረ፡፡
እንደ ጥጥ ቦጭቀህ አማኸው አትበሉኝና፣ ደመቀ በስካር መንፈስ ተገፋፍቶ ምን እንደፈፀመ ጠቆም ሳላደርግ አላልፍም፡፡
ፋሲካ ቡና ቤት፡፡ ደመቀ በሞቅታ ተገፋፍቶ ትንሹን አዋሽ ወይን ጠጅ ጉያው ስር ይወሽቃል። የጃኬቱን ዚፕ ዘግቶ ከቡና ቤቱ ሊወጣ በሩ ጋ ከመድረሱ፣ የወይን ጠጁ ጠርሙስ ከጉያው ሾልኮ ወለሉ ላይ ይከሰከሳል፡፡ ወይን ጠጅ ወለሉ ላይ የረጋ ደም መስሎ ተንጣለለ፡፡ ዌይተሩ ደመቀ ላይ ቡጢ አሳረፈበት፡፡ ሁለት የፊት ጥርሶቹ ረገፉ፡፡ በሕይወት ዘመኑ የረገፉበት ጥርሶች ብዛትም ወደ አምስት ከፍ ያሉት ያኔ ነበር፡፡
ደመቀ እየቀበጣጠረ ነው….”እንዲሁም በአጋጣሚ የምፈጽማቸው ስህተቶች….በቅርቡ በቤተሰብ ፊት የደረሰብኝን ቅሌት በአይንህ ያየኸው ነው”
ውድ አንባብያን - እኔ እከሌ ይህን በላ…ይህንን ለበሰ…እንዲህ አደረገ እያልኩ ማማት አልወድም። በተለይም የቤተሰብ ገበናን ለባዕድ መዘክዘክ ነውር ይመስለኛል፡፡ ቢሆንም ደመቀ በቤተሰብ ፊት የደረሰብኝ ቅሌት በሚል የጀመረውን ታሪክ የማሳወቅ የተራኪነት ግዴታ ያለብኝ ይመስለኛል - እህህ…ጉድ ነው!...
ነገሩ እንዲህ ነው…ደመቀ አንዷን የመንገድ ላይ ጅራሬ ክፍሉ ይዟት ይገባል፡፡ እንደገቡ የአበሻ አረቄ ለብርድ በሚል መጠጣት ይጀምራሉ፤ ልጅቷ አረቄውን በላይ በላዩ ስትግፍ አብሾዋ ይነሳባትና ብርጭቆውን ወለሉ ላይ ታደቀዋለች፡፡ ጥፍሯን አሹላ…ጥርሷን እያንቀጫቀጨች ደመቀን ልትቦጭቀው ይሁን ልትዘነጥለው ስትል በሩን ከፍቶ ለማምለጥ ተውተረተረ፡፡
አንገቱን አነቀችው፡፡ እንደ ብረት ከጠነከረው እጅዋ አንገቱን ማስለቀቅ አልቻለም፡፡ ትንፋሽ አጠረው - ወደ ሞት ወሰድ አደረገው - ጨርሶ እንኳን አልወሰደውም - መለስ አለ፡፡ እንደጦስ ዶሮ አሽቀንጥራ ወረወረችው፡፡ ያኔ ይመስለኛል ትንፋሹ መለስ ሲልለት የድረሱልኝ ጩኸቱን የለቀቀው። ከወንድሞቹ ጋር ደመቀ ክፍል ገባን፡፡ ልጅቷን አረጋጋናትና ሰከን አለች፡፡ ከመውጣቷ በፊት “ሂሣቤን” ስትል ጠየቀች…
“ምንሽ ተነካና ነው የሚከፈልሽ?!”  አሳፋሪው የደመቀ ድምጽ ከተወተፈበት ሥርቻ፡፡ 100 ብር ዳኒ ሰጣት፡፡ ግድንግድ ደዘደዝ፡፡ ይችን ቋጥኝ የምታክል መጋዣ፣ ኮስማናው ደመቀ ምንስ… እንዴትስ ሊያደርጋት ነበር? ደመቀ ይህን የመሰሉ በኮሜዲ ፊልም ላይ እንጂ በቤተሰብ መሐል መታየት የሌለባቸው ኮሚክ ስህተቶችን ሲፈጽም አመታት ያስቆጠረ የ47 ዓመት “ጉድ” ነው፡፡…
ለደመቀም ለእኔም ደብል ጂን አዘዝኩ…
“…ብሌን በእኔ ላይ ግፍ ሠርታለች…እንከን የሌለበት ማንም የለም….ግን የእኔ ኢምንት…ቅንጣት ስህተቶቼ ለምን እንደሚጋነኑብኝ…” አለ - ደመቀ። “ቅንጣት እንከኖቼ ትላለህ እንጂ እንከኑ አንተው ነህ” ብለው ልቡ ሊሰበር ይችላል ብዬ ተውኩት፡፡ ስለደመቀ ልብ ካነሳን አይቀር ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሳሳ ብላ እንደመደካከም እያደረጋት ነው - አንዳንድ ጊዜ በፍጥነት ደቅ! ደቅደቅ! ትልና እንደመቆ ይሁን መምታት ትንተፋተፋለች፡፡ ያኔ ዝልፍልፍ ብሎ አይኖቹ ግልብጥብጥ ይሉና ወሰድ ያደርገዋል፡፡ ጨርሶ እንኳን አይወስደውም፡፡ እንደ ደመቀ አይነት ሰዎች በቀላሉ ለሞት እጃቸውን አሳልፈው አይሰጡም። ከአደገኛ ጠጭነቱ ጋር የጨጓራ አልሠር፣ የጉበት መታወክ፣ …ደመቀ ከሚሰቃይባቸው በሽታዎች ይጠቀሳሉ፡፡ በፈርጀ ብዙ የጤና ቀውስ በመሰቃየት ወደ ሞት መለስ ቀለስ ማለቱ በመደጋገሙ፣ አብሮ አደግ ጓደኞቹ ሁሌም እንደመከሩት ነው - “ደመቀ መጠጥ አቁም አለበለዚያ አይናችን እያየ አፈር ሊበላህ ነው”…የህይወት ምፀት ግን፣ ደመቀ ሳይሆን አብዛኛዎቹ መካሪ ጓደኞቹ የአፈር ሲሳይ ሆነዋል። አብሮ አደግ ጓደኞቹ በሞቱ ቁጥር “ወይኔ ጓዴ! መካሪዬ!” እያለ ስቅስቅ ብሎ እያለቀሰ ስንቱን የቀበረ ሰው ነው፡፡ “አለሁ በለኝ መካሪዬ” የምትለዋ የደመቀ ሙሾ በብዙዎች ቀብር ላይ ተደጋግማ በመሰማቷ፣ ሰዎች ደመቀን መምከር ፈሩ፡፡ ደመቀን መምከር ማለት ለመላዕከ ሞት “ከዚች ምድር ገላግለኝ” የሚል ቴክስት እንደመላክ ተቆጠረ፡፡
ደብል ጂን ለሞት እምቢ - ለእኔም አዘዝኩ። ደመቀ ሞቅታ በፈጠረበት መንተፋተፍ “ለፍቅር ያኘሁት ምላሽ ክህደት ንቀት ነው…እድለ ቢስ ነኝ፤ በተራ ምክንያት የ3ኛ ዓመት ዩኒቨርስቲ ትምህርቴን ያቋረጥኩት በእድለቢስነቴ ነው… ሳግ ተናነቀውና ማንባቱን ተያያዘው፡፡ እንባው እንደደራሽ ውሃ በጉንጩ ኩልል አለ፡፡ እንባውን ሳይ ሐዘን ልቤን ጠቅ አደረገው - ምክንያቱም ደመቀ ሥካሩን በእምባው እያበረደ፣ በአዲስ ኃይልና ጉልበት እንደሚጨልጥ ከልምድ አውቀዋለሁ፡፡ ከዩኒቨርስቲ የ3ኛ አመት ትምህርቱን ማቋረጡ ሀቅ ነው - ከ25 ዓመት በፊት። ሩብ ምዕተዓመት መሆኑ አይደል!
የፈራሁት ደረሰ - ደመቀ ስካሩን በእንባው አብርዶ በአዲስ መንፈስ ጂኑን ይቀነድበው ጀመር። 6ኛ ደብል ጂን በራሱ ጊዜ አዘዘ፡፡ አልገረመኝም… “እንባህ ነው ጠላቴ” በሚል ርዕስ የተፃፈ ግጥም ይኖር ይሆን?...ደመቀ መቀበጣጠሩን ቀጥሏል። “የገዛ ህይወቴ ለእኔ እንቆቅልሽ ናት - ቤተሰቦቼ አይገቡኝም፤ የመኖር ጥበብ - የህይወት ሕግ አይገባኝም፤ አልገባኝም…ከአለም አቀፍ ሕግ ጋር መዋሀድ ሳይችል ቀርቶ ከምድረገጽ የጠፋው ዳይኖሰር ማለት እኔ ነኝ…የህይወቴ ክር መበጠሻው ቀርቧል…”
…በመሰላቸት አዛጋው…
“ከልብህ አዳምጠኝ…ከአንተ የተሻልኩ ሰው ነኝ…አለኝ ከምትለው መናኛ ድግሪ የእኔ የ3ኛ አመት ትምህርት አሥር እጅ ይበልጣል”
ሂሣብ ዘጋሁ፡፡ የህይወቴ ቅዠት ለሆነው ደመቀ የስድስት ደብል ጂን ሂሳብ ውስጤ እያረረ ከፈልኩ። ደመቀ እየደነፋ ነው… “የማንም ልቅምቅም - የሰው ልክ አያውቅም!”….
ምስኪን ነኝ - እድለቢስ…ሲል እንዳልነበረ እነሆ እኔን “የማንም ልቅምቅም” ከማለት ደርሷል ….ባጐረስኩ እጄን ተነከስኩ ቃል በቃል በእኔ ላይ ደረሰ፡፡ የመጨረሻዋን ጭላጭ ጨልጦ አፈጠጠብኝ። ዶቃ አይኖቹ አሁንም ለመጠጣት ያለውን ውስጣዊ ፍላጐት ያሳብቃሉ፡፡ እኔም በጥላቻ ትክ ብዬ አፈጠጥኩበት፡፡ ቡዳ ብሆን መሬት ላይ ጠብ ብሎ በተንደፋደፈ ነበር፡፡
ከግሮሠሪዋ ወጣን፡፡ ሞቅ ብሎኛል፡፡ ደመቀ ጢው ብሏል፡፡ …ቤት ልንደርስ ጥቂት ሲቀረን ደመቀ ዘፍ ብሎ መሬት ላይ ተቀምጦ ቀረ፡፡ “ተነስና እንሂድ”
“ወዴት ነው የምንሄደው?”
“ወደ ቤት እንግባ”
“ወደ መቃብር ነው መግባት የምፈልገው”
ሰዓቱ ገፍቷል - በዚያ ላይ ሠፈራችን ሕግና ፍትህ ዘግይተው የሚደርሱበት የእሪ በከንቱ እህት ከሆነ ቆይቷል፡፡ ጥዬው ልሂድ? ግራ ግብት ብሎኝ የደመቀን ዲስኩር ለመስማት ተገደድኩ፡፡ “ራሴን አንጠለጥላለሁ…ብሌንና ወንድሞቼ በእኔ ላይ የፈጸሙት ግፍ ትዝ እያላቸው በፀፀት እምባቸውን…ለእኔ እራስን ማጥፋት አዲስ አይደለም - ሞክሬዋለሁ…አልተሳካልኝም እንጂ…መኖርም መሞትም ያልቻልኩ…ወይኔ ደመቀ!”
…በቅርቡ በገመድ ቢጤ ተንጠልጥሎ ነበር። በቸልተኝነት ይሁን ከጥንቃቄ ጉድለት፣ ገመዱን ባግባቡ ስላልቋጠረው ቁልቁል ወለሉ ላይ በአፍጢሙ ተከሰከሰ…ደግነቱ የላይኛው ከንፈሩ ከመሰንጠቅ በቀር ከፊት ጥርሶቹ አንዱም አልረገፈም - የፊት ጥርሶቹ ከወራት በፊት በደረሰበት ቡጢ ስለመርገፋቸው የተረኩላችሁ መሰለኝ፡፡
ቤት ስንደርስ እኩለ ሌሊት አልፏል፡፡
…ሸለብ ሊያደርገኝ ሲል ከፍተኛ የማጓራት ድምጽ ብንን አደረገኝ፡፡ ወደ ደመቀ ክፍል ገባሁ፡፡ ደመቀ እያንቋረረ እያስመለሰው ነበር፡፡ የተቆራረጠ የረጋ ደም - ሙሉ ጉበቱን ተፋ ማለቱ ይቀላል፡፡ ወንድሞቹ ቢኒና ዳኒ ተሸማቀው ያዩታል፡፡ ደመቀ እየተንተፋተፈ “ወንድሞቼ፤ ሽንት ቤት በድብቅ ማስመለስ አላቃተኝም - በናንተ ፊት ደም የተፋሁት የመጠጥን ገዳይነት እንድታውቁት ነው - እኔን ያየ ተቀጣ” ደመቀ ትንፋሽ አጠረው መሰል ንግግሩን አቋርጦ ዳኒ ክንድ ላይ ዝልፍልፍ አለ፡፡ አልጋው ላይ ተሸክመን አጋደምነው፡፡ እንቅስቃሴ አልባ በድን ሆኗል፡፡ የወንድሞቹ አይኖች እንደ ጦር ወደ እኔ ሲወነጨፉ ተሸማቀቅሁ - “እንዲህ እስኪሞት ድረስ አጠጣኸው” በሚል፡፡
ደመቀ ለዘመናት ከስንቱ ትውልድ ጋር ሲጠጣ እንዳልኖረ ዛሬ በእኔ የግብዣ ጦስ ህይወቱ ሊያልፍ በቋፍ ነው፡፡ ብርክ ያዘኝ፡፡ “እኔን ያየ ተቀጣ” የሚለው ቃሉ የመጨረሻም ኑዛዜውም መሰለኝ። ለወንድሞቹም ህይወቱን አሳልፎ ክልትው ያለም መሰለኝ፡፡ ከዚህ የቁም ቅዠቴ ያወጣኝ ደመቀ “ውጡልኝ ልተኛበት” ብሎ ሲያንባርቅ ነው፡፡ እንኳን ህይወቱን የአንድ ቀን እንቅልፉን አሳልፎ ያልሰጠው ደመቀ፡፡
ድህረ ታሪክ
የክረምትን መግባት ተከትሎ የደመቀ የጤና ቀውስ ተባባሰ፡፡ ያቺ አመታዊ ሳል ተነስታ ታንተከትከው ጀመር፡፡ በቅዝቃዜ ሰውነቱ ራደ። “ለቅዝቃዜው” በሚል የሚወስዳት አረቄ ሰበብ፣ ጫና የበዛባት ጨጓራው ሆድ እየባሳት የአሲድ እንባዋን ትረጨውም ጀመር፡፡ እናም እንደቃር ይሁን እንደ ጣር እያንቋረረ ያስመልሰዋል፡፡ ሐሞት መሳይ ወደ ቢጫ የሚያደላ ዝልግልግ ትውከት፡፡ ሕመሙ ፋታ አልሰጥ ብሎት በጽኑ ቢሰቃይም፣ በሥራ አጥነትና በፍቅር ደረሰብኝ ከሚለው ሌላኛው ሐሳቡ አላቆት ይሆናል፡፡
የኢንዶስኮፕ ምርመራ ውጤቱ የጨጓራውን በከፍተኛ ሁኔታ መታወክ የሚያሳይ በመሆኑ የተወሰነ የጨጓራ ክፍሉ በኦፕራሲዮን መወገድ ግድ ሆነ፡፡……ከኦፕራሲዮን በኋላ ደመቀ ከገባበት ሰመመን መንቃት አልቻለም፡፡ ደቂቃ፣ ሰዓታት፣…እንደዘበት ነጐዱ፡፡ ነርሶቹ ባለመረጋጋት ወጣ ገባ ይላሉ፡፡
ዳኒና ቢኒ እየተንሰቀሰቀሱ ማንባት ጀምረዋል። አይ ደመቀ እድለቢስ፡፡ የዩኒቨርሲቲ ትምህርቱን ባቋረጠ አመት የእናቱ ህልፈት ቅስሙን ሰብሮታል። የብሌንን ፍቅር ማጣቱ፡፡ የተሰበረ ቅስም፡፡ የተሰበረ ልብ፡፡ ማን ከጐኑ ነበር - ማንም፡፡ ምንም፡፡ እነሆ የህይወት ወንዝ ከሞት ደለል ላይ… እንባዬን ልቆጣጠረው አልቻልኩም፡፡ በደመነፍስ ደመቀ ወደተኛበት ሪከቨሪ ክፍል አመራሁ፡፡ ነርሷ “ክልክል ነው” እያለች ብታንባርቅም ወደ ውስጥ ዘለቅሁ፡፡ የሚቀፍ የዝምታ አዚም ነግሷል፡፡ አየሩ በሞት ጠረን ታጅሏል፡፡ የደመቀ ህይወት አልባ በድን አካል ላይ አይኔ ተጣበቀ፡፡ ነርሷ በመደናገጥ “ለዚህን ያህል ሰዓት አለመንቃቱ አደጋ ነው…ተተኪውን ዶክተር ልጥራው” ብላ እግሯ ከመውጣቱ ደመቀ “በተተኪ የምትሠሩት ትያትር ነው እንዴ?” በማለት ከገባበት ሰመመን ነቃ  - ሰርፕራይዝ!
ውድ አንባቢያን - እንደደመቀ አይነት ሰዎች እንዲህ በቀላሉ ለሞት እጃቸውን አሳልፈው አይሰጡም - እየሳሱ - እየከሱ - እየከሰሙ…ከወንዝ ዳር እንደሚገኝ አለት እየተሸራረፉ ዘመናት ያስቆጥራሉ፡፡  

Published in ልብ-ወለድ

         በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደተሳለ የተነገረለትና ፓሪስ ውስጥ ከሚገኘው ‘ሚዩዜ ዲ ኢሆሜ’ ሙዚየም እኤአ በ1989 የተሰረቀው የቅዱስ ዮሃንስን ምስል የሚያሳይ ጥንታዊ የኢትዮጵያ ስዕል፣ ከሰሞኑ ዱሮውት በተባለ አጫራች ድርጅት አማካይነት ማይሰን ፒያሳ ውስጥ በተዘጋጀ ጨረታ ለሽያጭ ቀርቦ መገኘቱን ዘ ፊጋሮ የተባለው የአገሪቱ ጋዜጣ ባለፈው ሰኞ ዘግቧል፡፡
እኤአ በ1932 ማርሴል ግሪአውሌ የተባሉ የኢትኖግራፊ ባለሙያ ከዳካር እስከ ጅቡቲ ባደረጉት የጥናት ጉዞ በእጃቸው እንዳስገቡትና አባ አንጦንዮስ በተባለ ደብር ውስጥ እንደነበረ የተነገረለት ይህ ጥንታዊ የኢትዮጵያ ስዕል፣ ወደ ሙዚየሙ ከመግባቱ በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ ለተመልካች የቀረበው ፈረንሳይ ውስጥ በሚገኝ ቤተክርስቲያን ነበር ተብሏል፡፡
ባለሙያው ቤተክርስቲያኑ መሰል ጥንታዊና ውድ ስዕሎችን ለማሰቀመጥ ምቹ አለመሆኑን በመግለጽ ስዕሎቹን በዘይት ቀለም አስመስለው በማሰራት ለመተካትና ዋናውን ቅጂ ለማውጣት እንዲችሉ ያቀረቡት ጥያቄ በአካባቢው የቤተክህነት አስተዳዳሪዎች ፈቃድ ማግኘቱ የተገለጸ ሲሆን፣ በወቅቱ የኢትዮጵያ መንግስት የውጭ ጉዳይ ሚንስትር የስዕሉን ከቤተክርስቲያኑ መውጣት ቢቃወሙም የስልጣን ላይ የነበሩት የፈረንሳይ ንጉስ ግን ድጋፋቸውን ለባለሙያው መስጠታቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
በግለሰቡ እጅ ላይ ለተወሰነ ጊዜ ቆይቶ፣ ፓሪስ ውስጥ ወደሚገኘው ‘ሚዩዜ ዲ ኢሆሜ’ ሙዚየም እንዲገባ የተደረገው  ይህ ስዕል፣ እኤአ በ1989 ከሙዚየሙ የስዕል ስብስቦች መካከል ድንገት እንደተሰወረና ማን እንደሰረቀው ሳይታወቅ ደብዛው ጠፍቶ እንደኖረ ተነግሯል፡፡
ከ25 አመታት በኋላ ታዲያ፣ ጃክ ሜርሲየር የተባሉ በኢትዮጵያ ዙሪያ የተለያዩ ጥናቶችን በመስራት የሚታወቁ ምሁር ናቸው፣ ደብዛው ጠፍቶ የኖረውን ይህን ጥንታዊ ስዕል በጨረታ ሊሸጥ ቀርቦ ባለበት ሁኔታ ሰሞኑን ድንገት ያገኙት፡፡ የእኒህን ምሁር ጥቆማ የተቀበለው ሙዚየሙ አጫራቹን ድርጅት በማግኘት ስለጉዳዩ ያነጋገረ ሲሆን፣ ስዕሉን ለጨረታ ያቀረበችው ነዋሪነቱ በፈረንሳይ የሆነው የታዋቂው ኩባዊ ሰዓሊ ጃኪን ፌረር ባለቤት መሆኗ ታውቋል፡፡
 ሴትዮዋ ስዕሉ ከሙዚየሙ ከጠፋ ከጥቂት አመታት በኋላ ከአንድ ገበያ እንደገዛችው ተናግራለች፡፡ በወቅቱ ስዕሉን ከሙዚየሙ ማን እንደሰረቀውም ሆነ ለእሷ እንደሸጠላት አሁንም ድረስ የተጨበጠ ነገር አልተገኘም፡፡
ስዕሉ ግን ሙዚየሙ ከሴትዮዋ ጋር ባደረገው ስምምነት ሊሸጥ ከቀረበበት ጨረታ እንዲወጣ የተደረገ ሲሆን፣ በቀጣይም ኳይ ብራንሊ ውስጥ በሚገኘው የስዕል ማዕከል ውስጥ ከሚገኙት የሌሎች 11 ቅዱሳን ስዕሎች ጋር እንዲቀላቀል የሚደረግ መሆኑ ተገልጧል፡፡



Published in ጥበብ

የጣሊያኗ ቬነስ በአንደኛ ደረጃ ተቀምጣለች


ዩኔስኮ በአለም ቅርስነት ከመዘገባቸው የኢትዮጵያ ቅርሶችና የቱሪስት መስህቦች መካከል የሚጠቀሱት ጥንታዊ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙባት የላሊበላ ከተማ፣ ‘አንድ ሰው በህይወት ዘመኑ ሊያያቸው የሚገባቸው 50 ምርጥ የአለማችን ከተሞች’ በማለት ታዋቂው ሃፊንግተን ፖስት ጋዜጣ ከጠቀሳቸው ከተሞች ተርታ ተመደበች፡፡
ጋዜጣው በቅርቡ ሚኑቢ ዶት ኔት በተባለ ድረገጽ አማካይነት የአለማችን ጎብኝዎች የሚያደንቋቸውን ታላላቅ የቱሪስት መዳረሻዎች እንዲጠቁሙ በማድረግ ባሰባሰበው መረጃ፣ በጎብኝዎቹ ከተመረጡ 50 የአለማችን ከተሞች ዝርዝር ውስጥ ላሊበላ 17ኛ ቦታ ላይ መቀመጧን ታዲያስ መጽሄት በሳምንቱ መጀመሪያ ዘግቧል፡፡
ላሊበላ ከኢትዮጵያ ታላላቅ ቅዱስ ከተሞች አንዷ ናት ያለው ሃፊንግተን ፖስት፣ በውስጧ የያዘቻቸው ጥንታዊ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትም በመላው አለም የሚታወቁ ድንቅ መስህቦች መሆናቸውን ገልጧል፡፡
ከጥንታዊ የአገራት ርዕሰ መዲናዎች፣ እስከ እስያ ዘመናዊ ከተሞች በመላው አለም የተለያዩ ክፍሎች የሚገኙ ከተሞችን ባካተተው በዚህ ዝርዝር ውስጥ ቀዳሚነትን ያገኘችው የጣሊያኗ ቬነስ ናት፡፡ የሚያማምሩ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች፣ ገራሚ አብያተ ክርስቲያናት፣ ማራኪ ቤቶች፣ ምቾት የሚለግሱ መጠጥ ቤቶች ብዙ ብዙ ማራኪ ነገሮች የሞሉባት ቬነስ፣ ከአለም ከተሞች አምሳያ የሌላት ምርጥ ከተማ ናት ብሏታል ጋዜጣው፡፡
የስፔን ነገስታት መናገሻ ውብ ከተማ፣ ጎብኝዎች በብርቱካናማ አበቦች የተዋቡ ጠባብ መንገዶቿን ተከትለው በመጓዝ ማራኪ ጥንታዊ ህንጻዎችን አሻግረው እየቃኙ መንፈሳቸውን የሚያድሱባት አይነግቡና ቀልብ አማላይ ከተማ በማለት ሁለተኛ ደረጃ የሰጣት ደግሞ የስፔኗን ሲቪሊ ነው፡፡
 ኒዮርክ ሲቱን ሶስተኛዋ መታየት ያለባት የአለማችን ቀልብ ገዢ ከተማ ያላት ሃፊንግተን ፖስት፤ የትም ዙሩ የትም፣ እንደ ኒዮርክ ሲቲ መንፈስን ገዝቶ በአድናቆት የሚያፈዝ የኪነጥበብ፣ የባህል፣ የምግብ አሰራርና የንግድ እንቅስቃሴ በአንድ ላይ ተዋህደው የሚገኙባት ከተማ በየትኛውም የአለም ጥግ አታገኙም ብሏል፡፡
የህንዷን ላህሳ በመንፈሳዊ ማዕከልነቷና በማራኪ የተፈጥሮ ገጽታዋ፣ የብራዚሏን ሪዮ ዲ ጄኔሮ በውበቷ፣ የእንግሊዟን ለንደን በምርጥ ሙዚየሞቿና በጎብኝዎች ተመራጭ ከሆኑ የአለማችን ቀዳሚ ከተሞች አንዷ በመሆኗ በተከታታይ እስከ ስድስተኛ ያለውን ቦታ ሰጥቷቸዋል፡፡ የሞሮኮዋ ማራኬች፣ የዮርዳኖሷ ፔትራ፣ የጣሊያኗ ሮምና የህንዷ ቫራናሲም አንድ ሰው በህይወት ዘመኑ ሳለ ሳያያቸው ማለፍ የሌለባቸው ከተሞች ናቸው ተብለዋል፡፡

Published in ጥበብ

የቀድሞ ተማሪዎቹን የሚያሰባስብ ፅ/ቤት ሊከፍት ነው
ዩኒቨርሲቲው እስከዛሬ ከ40 ሺህ በላይ ተማሪዎችን አስመርቋል
622 መምህራን መኖርያ ቤት ተገንብቶላቸዋል

ዩኒቨርሲቲው እስከዛሬ ከ40 ሺህ በላይ ተማሪዎችን አስመርቋል
622 መምህራን መኖርያ ቤት ተገንብቶላቸዋል

የተመሰረተበትን 60ኛ ዓመት ያከበረው ጎንደር ዩኒቨርሲቲ፤ ከ35ሺህ የቀድሞ ምሩቃኖቹ መካከል ከ500 በላይ የሚሆኑትን በድጋሚ ያስመረቀ ሲሆን የቀድሞ ተማሪዎችን የሚያሰባስብ ጽ/ቤትም ይከፈታል ተብሏል፡፡
ዩኒቨርሲቲው 60ኛ ዓመቱን ምክንያት በማድረግ በተለያዩ የስራ መስኮች ተሰማርተው የሚገኙ 1ሺህ ያህል የቀድሞ ምሩቃኖቹን በልዩ ስነ-ስርአት በድጋሚ ለማስመረቅ ጠርቶ የነበረ ሲሆን ከግማሽ በላይ የሚሆኑ ተገኝተው የስነ-ስርአቱ ታዳሚ ሆነዋል፡፡ የቀድሞ ተማሪዎችን በድጋሚ ለማስመረቅ ያስፈለገበትን ምክንያት ያስረዱት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ፕ/ር መንገሻ አድማሱ፤ “እውቀት የቀሰሙበት ዩኒቨርሲቲ ምን ደረጃ ላይ እንደደረሰ እንዲያውቁትና ለዩኒቨርሲቲያቸው የተቻላቸውን አስተዋፅኦ እንዲያበረክቱ ለማድረግ ነው” ብለዋል፡፡ በቀጣይም ስለቀድሞ ተመራቂዎችና ከዩኒቨርሲቲው ተመርቀው በስራ ላይ ስላሉት ምሩቃኖች ሙሉ መረጃ አሠባስቦ በመያዝ፣ ተማሪዎቹ ምን ደረጃ ላይ እንደደረሱ ክትትል የሚያደርግ ጽ/ቤት ለማቋቋም ዩኒቨርሲቲው ማቀዱን ፕሬዚዳንቱ ገልፀዋል፡፡
“ዩኒቨርሲቲውን ከአፍሪካ ቀዳሚዎች ተርታ ለማሰለፍ እየሰራን ነው ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ ለውጭ ሃገር ዜጎች ባመቻቸው የትምህርት እድልም ከጅቡቲና ከሶማሊያ 25 የህክምና ተማሪዎችን ተቀብሎ 17 ያህሉን ለመጀመሪያ ጊዜ ባለፈው ቅዳሜ በተካሄደው የምረቃ ፕሮግራም ላይ አስመርቋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው በቀጣይም ከደቡብ ሱዳን ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማሰልጠን እቅድ መያዙን ፕሬዚዳንቱ አክለው ገልፀዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በትምህርት ጥራቱ በተለያዩ ጊዜያት በተሰጡት ደረጃዎች በኢትዮጵያ ካሉት በ2ኛ እና 3ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠ ቢሆንም የመማር ማስተማር ሂደቱም ሆነ የትምህርት ጥራቱ ውጤታማ ነው ብለን እናምናለን ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ ከሌላው ዩኒቨርሲቲ በተለየ የመምህራኖች በዩኒቨርሲቲው ተረጋግቶ መቆየት ሂደቱን ውጤታማ አድርጎታል ብለዋል፡፡ አስተዳደሩም የመምህራኑን ምቾት ለመጠበቅ ሲል በ220 ሚሊዮን ብር ገደማ እዚያው ጐንደር ከተማ አዘዞ አካባቢ ባለ 31 ብሎክ ህንፃዎችን አስገንብቶ ለ622 መምህራን የመኖሪያ ቤቶችን በቅርቡ እንደሚያስረክብ ፕሬዚዳንቱ አስታውቀዋል፡፡
የዩኒቨርሲቲው መምህራን ከዩኒቨርሲቲው ከሚያገኙት ደመወዝ ባሻገር እዚያው ጎንደር ከተማ ሃኪሞቹ የራሳቸውን ክሊኒክና የተለያዩ ስራዎችን በትርፍ ጊዜያቸው መስራታቸው ለመምህራኑ ገቢ ማደግ አስተዋፅኦ እንዳለው የጠቀሱት ፕሬዚዳንቱ፤ ዩኒቨርሲቲው መምህራኑ በተጓዳኝ ገቢ የሚያገኙበትን የስራ መስክ እንዲፈጥሩ ያበረታታል ብለዋል፡፡
የዩኒቨርሲቲው ግቢ ለመማር ማስተማሩ ሂደት የተመቻቸ እንዲሆን የተለያዩ የአካባቢ ጥበቃ እና የመናፈሻ ስራዎች ከመሰራታቸው ባሻገር በግቢው ላይ የዋይ ፋይ ኢንተርኔት አገልግሎት በማንኛውም ቦታ እንዲገኝ ተደርጓል ብለዋል ፕሬዚዳንቱ፡፡
በዘንድሮው አመት በተለያዩ የትምህርት መስኮች የተመረቁትን 4135 ተማሪዎችን ጨምሮ ዩኒቨርሲቲው በ60 ዓመት ጉዞው ወደ 40 ሺህ ተማሪዎችን ያስመረቀ ሲሆን ከጤና ኮሌጅነት ተነስቶ በአሁን ሰዓት ዘጠኝ ፋኩልቲዎች፣ ኮሌጆች እና ት/ቤቶች አሉት ተብሏል፡፡ 60ኛ ዓመቱን ለማክበር 8 ሚሊዮን ብር ገደማ እንዳወጣ የጠቆሙት ፕሬዚዳንቱ፤ ወጪው የተጋነነ አይደለም፤ የዩኒቨርሲቲውን አርማ ከያዙ ቲ-ሸርቶች፣ እስክርቢቶና ከረቫት እንዲሁም የዩኒቨርሲቲውን የ60 ዓመት ጉዞ ከሚያስዳስሰው መፅሃፍ ሽያጭ ወጪውን እንመልሳለን ብለዋል፡፡
በዩኒቨርሲቲው ስር የሚተዳደረው የጎንደር ሪፈራል ሆስፒታል የተመላላሽ ታካሚዎች ሆስፒታል በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የተመረቀ ቢሆንም ሥራ ለመጀመር የሚያስችሉ የህክምና መሳሪያዎችና አልጋዎች እንዳልተሟሉለት ታውቋል፡፡ ለሆስፒታሉ የሚስፈልጉ ውድ የህክምና መሳሪያዎችን ጨምሮ የተለያዩ ቁሳቁሶችን ለመለገስ ቃል እንደተገባ ለማወቅ ተችሏል፡፡
“ጐንደር ዩኒቨርስቲና የገበሬዎቹ ውለታ”
የዛሬው ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ለመመስረቱ ምክንያት የሆነው የወባ በሽታ ነው፡፡ ከ60 ዓመት በፊት ጎንደር ደንቢያ ላይ 20ሺህ ሰዎች በወባ መጠቃታቸውን ተከትሎ ዩኤስ ኤይድ፣ ዩኒሴፍ፣ የአለም ጤና ድርጅት እና የኢትዮጵያ መንግስት በጋራ በመሆን ለተጎጂዎች ህክምና የሚሰጥበትን ጤና ጣቢያ ቆላ ድባ በተባለ ቦታ ከፈቱ፡፡ በኋላም እዚያው የማህበረሰብ ጤና አጠባበቅ ኮሌጅ ተመሰረተ፡፡ ከዚያው ወደ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ደረጃ አድጎ ከ10 ዓመት በፊት ሙሉ ለሙሉ ዩኒቨርሲቲ ሆነ፡፡ በኮሌጅ ደረጃ ሲመሰረት በዚያው በጎንደር ሆስፒታል ግቢ ውስጥ የነበረ ሲሆን ኋላም የማስፋፋት እቅድ ሲመጣ ማራኪ በሚባለው የከተማ አካባቢ ነዋሪ የነበሩ 59 ገበሬዎች “ልጆቻችን የትም ሳይሄዱ እዚሁ ትምህርት ማግኘት ከቻሉ፣ በነፃ ቦታውን እንሰጣለን” በማለት ቦታውን በ1963 ዓ.ም በነፃ ሰጡ፡፡ አፄ ኃይለሥላሴም የመሰረት ድንጋዩን ካኖሩ በኋላ ቦታውን ማራኪ ብለው ሰየሙት። እነዚያ ገበሬዎች በሰጡት ቦታ ላይ ዛሬ የማራኪ ካምፓስን ጨምሮ ቴዎድሮስና ፋሲል የተባሉ ሶስት ካምፓሶች ተገንብተውበት ለትምህርት አገልግሎት ውሏል። ዩኒቨርሲቲው ገበሬዎቹ አሊያም የገበሬዎቹን ቤተሰቦች አግኝቶ በሰፊው የመዘከር ሃሳብ እንደነበረው የጠቆሙት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት፤ በተለያዩ ምክንያቶች ሙሉ ለሙሉ ባይሳካም በየጊዜው በሚወጡ መፅሄቶች እና የዩኒቨርሲቲውን ታሪክ በያዙ ፅሁፎች ላይ እንደሚያስታውሷቸው ገልፀዋል፡፡

Saturday, 12 July 2014 12:30

የግጥም ጥግ

ላለ - መጨቆን
ሞት ይቅር ይላሉ…
    ሞት ቢቀር አልወድም
ከድንጋይ ---ቋጥኙ---
    ከሰው ፊት አይከብድም፡፡
ማጣት ክፉ ክፉ፤
ችግር ክፉ ክፉ፤
ተብሎ ይወራል
ከባርነት ቀንበር
ከሬት መች ይመራል፡፡
***
ለ- ጅገና
ተው! ተመለስ በሉት
ተው! ተመለስ በሉት!
ያንን መጥፎ በሬ
ከጠመደ አይፈታም ያገሬ ገበሬ
* * *
ያባቴ ነው ብሎ፤
የናቴ ነው ብሎ፤
ይፋጃል በርበሬ
አባት የሌለው ልጅ፤
እናት የሌለው ልጅ፤
አይሆንም ወይ አውሬ
ለወንድ - አደር
ዓይንሽ የብር ዋጋ
ጥርስሽ የብር ዋጋ
    ወዳጆችሽ በዙ ከስንቱ ልዋጋ?
(ከክፍሌ አቦቸር (ሻምበል)
“አንድ ቀን” የግጥም መድበል፤ 1982፣ የተወሰዱ)

Published in የግጥም ጥግ

ባለፈው ሳምንት “ስማርት” ስለተባሉት የቢዝነስ መመሪያዎች ስንነጋገር፣ በአሁኑ ወቅት ሕይወትም ሆነ ቢዝነስ ያለእቅድና ግብ አይመራም ብለን ነበር። በዚህ ሳምንት ቀጣዩን ክፍል ነው የማቀርበው፡፡
ለሕይወታችንና ለቢዝነስ የምንቀርፃቸው ግቦች በሁለት ይከፈላሉ፡፡ አንደኛው ግብ በአብዛኛው ከአሁን ቀደም የሰራነውና የምናውቀው ስለሆነ 95 በመቶ ይሳካል ብለን የምንቀ    ርፀው ነው፡፡ ሌላኛው ደግሞ ቀደም ብለን በፍፁም ያልሞከርነውና የማናውቀው ስለሆነ ያለመሳካት ዕድሉ 95 በመቶ ሊሆን ይችላል፡፡ ግን ልንሰራውና ልንሞክረው እንፈልጋለን፡፡ ዝርዝር ውስጥ ባንገባም ሁለቱም የቢዝነስ ግቦች በራሳቸው መንገድ ጠቀሜታ አላቸው፡፡
የግብ ዕቅድ በማንኛውም መንገድ ሊዘጋጅና ሊፃፍ ይችላል፡፡ የዚህ ጽሑፍ መጠነኛ ትኩረት ግብ ቀረፃ ላይ ቢሆንም በአብዛኛው ግን፣ ግቡን በመፈፀም ሂደት ላይ የበለጠ ያተኩራል ይላሉ፤ ሚ/ር ስኮት ሃልፎርድ፣ በጁን በታተመው ኢንተርፐሪነር መጽሔት ላይ ባቀረቡት ዘገባ፡፡
ጸሐፊው በማከልም “የቀረፃችሁት ግብ በእርግጥ ጠቃሚ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን ሊሳካ የሚችልባቸውን አንዳንድ ሁነኛ የስኬት ምክንያቶች ብትመርጡ እመርጣለሁ፡፡ ምክንያቱም ለዓላማና ግባችሁ ጠንካራና ጎበዝ መሆናችሁን ታዩበታላችሁ። የሰው ልጅ አዕምሮ፣ እርግጠኛ ሆነው ይሳካል ብለው ያመኑበትን ግብ ለማሳካት የተቃኘ ነው” ብለዋል፡፡ ስለዚህ በንግድ ሥራ ለመመንደግ ወይም ቢዝነሱን ወደ አዲስ ከፍታ ለማምጠቅ ከፈለጉ፣ ጸሐፊው ለከፍተኛ ስኬት ያበቃሉ ያሏቸውን ሰባት ነጥቦች እነሆ!
የተነቃቃ ሕልም ለትልቅ ግብ - ቤት፣ መኪና፣ ትምህርት፣… ማለም ጥሩ ነው፡፡ ነገር ግን እርግጠኛ ሆነው ተግባራዊ የሚያደርጉት ከሆነ ለዚያ ሥራ የሚያተጋ (የሚነቃቃ) ነገር ያስፈልጋል፡፡ የመጀመሪያው ነገር፣ ሕልሙ ላይ ለመድረስ የሚያነሳሳ ምክንያትና ጥልቅ ፍላጎት ነው፡፡
ግብዎ ጋ የሚያደርሰው መንገድ አሰልቺ፣ ችግርና መሰናክሎች የተጋረጡበት ሊሆን ይችላል፡፡ ካሰቡበት ህልም እንዳይደርሱ የሚጋረጡ በርካታ አጋጣሚዎች (ችግሮች) ሊኖሩና ሊፈጠሩ ይችላሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ሊረዳዎትና ሊያጠነክርዎት የሚችለው ግቡ ላይ ለመድረስ ያነሳሳዎትን ምክንያት ማሰብ ነው፡፡
የሚከወኑትን ነገር ለ24 ሰዓት ይከፍላሉ፡- ግብዎ ከክብደትዎ 10 ኪሎ መቀነስ ከሆነ አዕምሮዎ የሚያውቀው በ24 ሰዓት 10 ኪሎ መቀነስ ሳይሆን በወሰኑት ጊዜ ውስጥ 500 ግራም መቀነስዎን ነው፡፡ ስለዚህ፣ ግብዎን አዕምሮዎ እንዲረዳ አድርገው ይቅረፁ፡፡ ሕልምዎ ሀብታም መሆንና መኪና መግዛት ከሆነ፣ እንዴት አድርገውና በምን ያህል ጊዜ ውስጥ ሀብታም እንደሚሆኑ (በየወሩ እቁብ እየጣሉ፣ ንብረት ሸጠው፣ ውርስ ተካፍለው፣ ደሞዝ አጠራቅመውና ተጨማሪ ገቢ ፈጥረው፣… በአንድ፣ በሁለት፣ በአምስት ዓመት፣ …) ተብሎና ተዘርዝሮ መቀመጥ አለበት፡፡ በጊዜ የተከፋፈለችው ትንሿ ግብ፣ ምክንያታዊና ቀጣይነት ያላት መሆን አለባት፡፡
በየወሩ ከደሞዜ 1000 ብር እየቆጠብኩ በዓመት 12 ሺ ብር ይኖረኛል፡፡ በአምስት ዓመት ደግሞ 60 ሺ ይኖረኛል፡፡ ተጨማሪ ሥራ በመስራት በወር 10ሺ ብር፣ በዓመት 120 ሺ ብር፣ ከአምስት ዓመት በኋላ 600ሺ ብር፣… ተብሎ ግብ ከተበጀ፣ በምንም ዓይነት ምክንያት ከዕቅዱ መዛነፍ የለበትም ማለት ነው፡፡
 በየቀኑ የሆነ ነገር ይሥሩ፡- ካሰቡት ግብ ላይ ለመድረስ፣ በየቀኑ ከሚያደርጉት የሥራ ድግግሞሽና ፍጥነት የበለጠ ምንም ዓይነት ነገር ወደ ግብዎ አያቀርብዎትም፡፡ ይህ ሲባል ግን ታምመው ቢተኙ እንኳ ከዕለታዊ ሥራዎ መቅረት የለብዎትም ማለት አይደለም፡፡ ከአቅም በላይ የሆነ ነገር ሲያጋጥም ወይም ሲደብርዎት ሊያቋርጡት ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ግብዎ ጋ ለመድረስ የመጀመሪያዎቹን 30 ቀናት በሚገባ ካልተጠቀሙና የአካሄድዎን ፍጥነት ካልለኩ 90 ከመቶ ግብዎን እንደማያሳኩ ማረጋገጫ ይሆናል፡፡ ስለዚህ፣ የመጀመሪያዎቹ 30 ቀናት ቁርጠኛ እንደሆኑ አዕምሮዎን ለማሳመን እጅግ ወሳኝ ናቸው፡፡
መቀየርና ማስተካከል (Adapt and Adjust)፡- ትልቁ ግብ ላይ ለመድረስ የሚችሉበትን ትንሿን የዕለት ተዕለት ግብ ሲተገብሩ፣ አመቺ ያልሆነ አስቸጋሪ ሁኔታ ሲያጋጥም፣ ሁኔታውን ማስተካከል ያስፈልጋል፡፡ የየዕለቱ ትንሿ ግብም በጣም ቀላል ከሆነች ጥሩ አይደለም። አተገባበሩ በጣም ቀላል ከሆነ የበለጠ ከበድ ያድርጉት፡፡ በአጠቃላይ፣ ወዳሰቡት ግብ ለመድረስ የሚደረገው ትግልና ጥረት ከባድ ከሆነ ደግሞ ቀለል ያድርጉት፡፡
የሰው አስተያየትና ሽልማት (Feedback and Reward)፡- የሰው ልጅ አዕምሮ፣ አዲስ ነገር ለመማርና አዲስ ባህርይና እውቀት ለመቅሰም ሁለት ነገሮች ያስፈልጉታል፡፡ አንደኛው አስተያየት (Feedback) ሲሆን፣ ሌላኛው ሽልማት (Reward) ነው፡፡
ግብዎን ለማሳካት ሲንቀሳቀሱ፣ የሌሎች አስተያየት ምን እንደሆነ ለመጠየቅ ድፍረት ይኑርዎት፡፡ “ይኼን ነገር እንዴት አየኸው? ምኑ መስተካከል አለበት ትላለህ/ትያለሽ?...” ብሎ መጠየቅ፣ ስህተትን አውቆ ለማስተካከል በጣም ጠቃሚ ነው፡፡ የሰዎች አስተያየት ጥሩ ከሆነና ወደ ግብዎ ለመድረስ ትክክለኛ መስመር ላይ ከሆኑ ጥሩ ነው፣ በየዕለቱ ትንሿን ግብዎን ያለስህተት ስላከናወኑ፣ እውቅና እንዲሆንዎ ራስዎን ይሸልሙ፡፡
ውጤታማ ሥራ ባከናወኑበት ቀን፣ ትንሽ ወርቃማ የኮከብ ምልክት የሚያደርጉበት ቀን መቁጠሪያ ቢኖርዎ ለበለጠ ለትጋት የማነሳሳት አቅም እንዳለው በጥናት ተረጋግጧል፡፡ ትክክለኛ ሥራ እያከናወኑ መሆኑን መገንዘብ ለአዕምሮ በቂ ሽልማቱ ነው፡፡         
በትኩረት ያልሰሩበትን ጊዜ ይለዩ (Schedule Slop Time):- ላቀዱት ግብ ትኩረት ያልሰጡበትን ወይም ራስዎን ያታለሉበትን ወይም ጭራሽ ያልሰሩበትን ጊዜ መዝግበው ይያዙ፡፡ ምክንያቱም፣ ያንን የባከነ ጊዜ ተመልሰው ስለሚሰሩ፣ ለጊዜው ተግባርዎን ያለመወጣትዎ ሊያሳዝንዎትና ሊያሸማቅቅዎት አይገባም፡፡ ግን ልማድ እንዳይሆን በጣም ይጠንቀቁ፡፡
መሰልቸት እንዳለ ይወቁ፡- አንድን ነገር በየቀኑ ትንሽ ትንሽ መሥራት ሊያሰለች ይችላል። ቢሆንም ግን አያቋርጡ፡፡ ምክንያቱም፣ ያቀዱት ግብ ላይ መድረስ፣ በየቀኑ የደስታ ሻምፓኝ የመክፈት ሥነ-ሥርዓት ያህል ቀላል አይደለም፡፡ ብዙ ጊዜ በየቀኑ ጥቃቅን ነገሮች ላይ አጣብቆ የሚያውል አሰልቺ ነገር መሆኑ መታወቅ አለበት፡፡ ይህን ነገር ተገንዝቦ በየቀኑ ትንሽ ጠንከር አድርጎ ደጋግሞ መስራት ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም ግባቸውን የሚያሳኩ ሰዎች፣ ነገሮች ከባድና አሰልቺ ሲሆኑባቸው ብዙ ጊዜ የሚያደርጉት እንደዚያ ነውና፡፡  

      ህፃን ሚሚ ጠባየ-ወርቅ ናት፡፡ ፎለፎል ናት። ሥራ ስትሰራ ጠንቃቃ ናት፡፡ ለመታዘዝ ዝግጁ ስለሆነች ለማዘዝ ቀለል ያለች ናት፡፡
ሚሚ ኃይሉ ከልጅነቷ ጀምሮ ወገቧና ትከሻዋ መካከል ባለ አኳላ ላይ የወጣው ትርፍ ጉባጭ  (Hunchback) በሰውነቷ ላይ ይታያል፡፡ ለግላጋ ቀይ ቆንጆ ልጅ ነች፡፡
ሚሚ ሀይሉን ልናነጋግራት እንደምንፈልግ ለአቶ ዓለምሰፋ ባለቤት ለወ/ሮ ገነት ስንጠይቃቸው “በደስታ! እጠራላችኋለሁ” ብለው ወደ ሚሚ ደወሉ። ሚሚ የ13 አመት ታዳጊ ህፃን ናት። የተወለደችው ጉራጌ ውስጥ ዶባ የሚባል ቦታ ነው። አዲስ አበባ የመጣችው በ2000 ዓ.ም ነው። ያኔ የስድስተኛ ክፍል ተማሪ ነበረች፡፡ አዲስ አበባ ከመጣች በኋላም ትምህርቷን ቀጥላለች፡፡ የአጎቷ በሆነውና ካዛንቺስ በሚገኘው “አለምሰፋ ሥጋ ቤት” ውስጥ ጊዜ ሲኖራት በመምጣት ስራ የምታግዘው ሚሚ፤ ሳታስበው ነው በዚያው ምግብ ቤት ህይወቷን የሚለውጥ አጋጣሚ የተፈጠረው፡፡
“ፈረንጆቹ ለወገቤ መድሀኒት እንዳለ ነገሩኝና ወገቤን ለመሰራት (ትርፍ አካሉን አስወግዶ ማስተካከል) ወደ ጋና ሄድኩ፡፡ በአውሮፕላን መሄድ ያስፈራል፤ ልቤ በጣም ፈራ፡፡” (ያም ሆኖ ሚሚ ጋና በሰላም ደረሰች፡፡)
“ሆስፒታል ገብቼ ህክምናው ከተካሄደልኝ በኋላ፤ “በጣም ደስ አለሽ ወይ?” አሉኝ፡፡ እኔም በጣም እንደተደሰትኩ ነገርኳቸው፡፡ ወገቤ ላይ ወጥቶብኝ የነበረውን ትርፍ ጉባጭ (Hunchback) አካል በማደንዘዣ ለማስወገድ ሲሰሩልኝ አልተሰማኝም ነበር፡፡ ስነቃ በጣም አመመኝ፡፡ ወገቤን ስለተሻለኝ ግን ደስ ብሎኛል፡፡ ወገቤ ያበጠ ስለነበር ጠፍቶ ሳየው በጣም ደስ አለኝ፡፡ ዶክተሩን አመሰግናለሁ” ስለው “ምንም ማለት አይደለም” አለኝ፡፡ እኔ ድሮም ቢሆን ከተማርኩ በኋላ ሀኪም መሆን እፈልጋለሁ ስል ነበር፡፡ እንደሌሎች ጤነኛ ሰዎች ስለሆንኩ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡
ወገቤን እንድታከም ያደረጉትን ሰዎች በሙሉ በጣም አመሰግናለሁ፡፡ በተለይ መንክርን (ባርቾን) በጣም አመሰግነዋለሁ፡፡
ባርቾ (መንክር) ስለሚሚና ህክምናዋ ምን ይላል?
መንክር ይርጋ የሚሚ የአክስት ልጅ ነው፡፡ ወደ ጋና ለህክምና ስትሄድ ሀላፊነቱን በመውሰድ የፈረመውም እሱ ነበር፡፡ ሚሚ ስላገኘችው እድል የሚከተለውን አጫውቶናል፡፡
ሚሚ ሰው ስትንከባከብ እንደ እናት ናት፡፡ በትምህርቷም ጎበዝ ናት፡፡ ጀርባዋ ላይ በነበረው እብጠት ምክንያት ቶሎ ሆድ ይብሳት ነበር፡፡ እብጠቱ ከጊዜ በኋላ ቀስ እያለ እየጎላ የመጣ ሲሆን ከዚህ በፊት ምንም አይነት ህክምና አድርጋ አታውቅም።  ሚሚ እንደሁልጊዜው ስራ እያገዘችን ነበር፡፡ ለደንበኞች ትኬት እየሰጠች ገንዘብ ትቀበላለች። በዚህ መሀል የቤቱ ደንበኞች የሆኑ የውጪ አገር ዜጎች ያዘዙት ምግብ እስኪመጣ እየጠበቁ ባሉበት ሰአት ሚሚን አይዋትና በአስተርጓሚያቸው አማካኝነት “ስለዚህች ልጅ የምናነጋግረው ሰው ጥሩልን” አሉ፤ እሷም እኔን አስጠራችኝ፡፡ ሄጄ ሳናግራቸው ሚሚ የምትታከምበት እድል እንዳለና ፈቃደኛ እንደሆንን ጠየቁኝ፡፡ ያለምንም ማመንታት ተስማማሁ፡፡ ጀርባዋ ላይ ያለው እብጠት መንስኤ ከቲቢ ጋር የተያያዘ እንዳይሆን ተብሎ ስድስት ወር የቲቢ ህክምና አደረገችና የጋና ጉዞዋ እንቅስቃሴ ተጀመረ፡፡  ከመሄዷ በፊት የሚፈረም ሰነድ ስለነበር፣ ፈርሙ ሲሉን ትንሽ ፈራን፡፡ ምክንያቱም ከዚህ በፊት ሰዎች ይዘው ሄደው የሞተና ፓራላይዝድ የሆኑ እንዳሉ እንዲሁም በህክምና ላይ ድንገት ህይወቷ ቢያልፍ አስከሬኗ እዚህ እንደማይመጣ ስለነገሩን ሰግተን ነበር፡፡ በኋላ ግን አደራውን ለፈጣሪ ሰጥተን ላክናት፤ እሱም አላሳፈረንም፡፡ ሚሚ እንደ አዲስ እንደተፈጠረች ነው የሚቆጠረው፡፡
የፈረንጆቹ አስተርጓሚ ራሱ እንደ ሚሚ ትርፍ ጉባጭ (Hunchback) የነበረው ሲሆን ታክሞ ነው የዳነው፡፡ ዛሬ ከፈረንጆቹ ጋር ይሰራል፡፡
ስለልጆች ጨዋታ ስትጠየቅ፤ “ገመድ መዝለል በጣም የምወደው ጨዋታ ነው!፡፡” ትላለች፡፡ ስለአካላዊ ሁኔታዋ ስታስታውስም፤ “የትምህርት ቤት ጓደኞቼ ምን ሆነሽ ነው ሲሉኝ በጣም አለቅስ ነበር፡፡ ሀኪሙ ረጅም መንገድ መሄድ ትችያለሽ ካለኝ በቅርቡ አገር ቤት እሄዳለሁ፡፡ እናት እና አባቴን በጣም ናፍቄያቸዋለሁ፡፡ እኔ በጣም መሄድ ፈልጌያለሁ፣ተሽሎኝ እንዲያዩኝም እፈልጋለሁ፡፡ በስልክ እንደታከምኩ ስነግራቸ፣ ለእግዚአብሄር ምን ይሳነዋል አሉ፡፡ ጓደኞቼም ሰምተዋል፤ በጣም ደስ ብሏቸዋል፡፡
ጋና ሳለች ምን ትመገብ እንደነበር ጠየቅናት “ጋና ምግቡ በብዛት ሩዝ ስለሆነ እንጀራ በጣም ናፍቆኝ ነበር፡፡ ዝላይ ከአመት በኋላ ስለሚፈቀድልኝ ያኔ እዘላለሁ፡፡ ኳስ መጫወትም እወዳለሁ፡፡ የብራዚል ደጋፊ ነኝ፡፡ ሲሸነፉ ላለቅስ ነበር፤ ከዚያ ተውኩት፡፡ ፑሽ-አፕ መስራትም እወዳለሁ፡፡” ስትል መለሰችልን።
የሚሚ ሀይሉ አሳዳጊ አቶ ዓለምሰፋ ኤርማቶ (የዓለምሰፋ ሥጋ ቤት ባለቤት) ሚሚ ወደ ጋና ስትላክ የመኖሪያ ቀበሌው ጽህፈት ቤት አስፈላጊውን የመሸኛ ደብዳቤ በመፃፍ ያደረገላትን ትብብር አድንቀዋል “ሁሉም ቀበሌዎች እንደሚሚ ዕድል ላገኙ ታማሚዎች ድጋፍ ማድረጋቸው ትልቅ ነገር ነው፡፡ ሚሚን ወስጄ ላሳያቸው እፈልጋለሁ፡፡” ብለዋል፡፡  

Published in ዋናው ጤና

ከወንድወሰን ተሾመ የማህበራዊ ሳይንስና የስነ ልቦና ባለሙያ
 (ከአልታ ምርምር ሥልጠናና ካውንስሊንግ)
ጭንቀት ምንድን ነው?
ጭንቀት የሰውነትን ተፈጥሯዊ ሚዛን የሚያዛባ የአካል፣የአዕምሮና የስሜት ትንኮሳ(stimulus) የሚፈጥረው  ምላሽ፣ ወይም የአንድ ሰው  ፍላጎት (demand) ሊያንቀሳቅሰው ከሚችለው የግልና የማህበራዊ ሃብቶች አቅም በላይ ሆኖ ሲታየው የሚፈጠር ስሜት፣  ወይም ነገሮች ና ሁኔታዎች ከቁጥጥራችን  እንደወጡ ስናስብ የሚፈጠር ስሜት ነው፡፡
መጠኑና ጊዜው ይለያይ እንጂ ጭንቀት የማይነካው ሰው እንደሌላ ይታወቃል፡፡ በአንድ ወቀት በአንድ ኮሌጅ ውስጥ የሳይኮሎጂ ኮርስ ሳስተምር አንድ ተማሪ አንድ ከፍተኛ ባለስልጣንን ጠቅሶ “እንዴት እሳቸው ይጨነቃሉ?” በማለት ሰውየው ከማንኛውም ጭንቀት በየትኛውም ሁኔታና  ጊዜ ነፃ ናቸው ብሎ እንደሚያምን ገልጾ እንደተሟገተ ትዝ ይለኛል፡፡ ሆኖም በየትኛውም የስልጣን እርከን ወይም የሥራ ሃላፊነት ላይ ብንሆን በጥቂቱም ቢሆን በተለያየ ጊዜና ሁኔታ ጭንቀት ወደ እኛ ሊመጣ ይችላል፡፡ የሚወጡ ሳይንሳዊ መረጃዎች ደግሞ ሃላፊነትና ውሳኔ ሰጪነት ሲጨምር ጭንቀት እንደሚጨምር ይጠቁማሉ፡፡ ለዚህም ነው ባለስልጣናት፣ ስራ አሰኪያጆች፣ ዲሬክተሮች፣ ሥራ ሃላፊዎች በጭንቀት መቆጣጠሪያ (stress management strategies) ስልቶች እንዲሰለጥኑ መደረግ ያለበት፡፡ በማንኛውም ደረጃ የሚሰራና ከስራ ውጪም የሆነ ሰው የጭንቀት መቆጣጠሪያ  ስልቶችን መሰልጠኑ፤ማወቁና መተግበሩ የተረጋጋ ህይወት እንዲመራ ይረዳዋል፡፡ ጭንቀት ውሳኔን የማዛባትና ትኩረትን የመቀነስ ሃይል ስላለው የጭንቀት መቆጣጠሪያ ስልቶችን ማወቅና መሰልጠን ይገባቸዋል፡፡
የጭንቀት ምንጮች ምንድን ናቸው?
የጭንቀት ምክኒያቶች በርካታ ናቸው፡፡  ሆኖም  በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች ለይቶ ማየት ይቻላል፡- አካላዊና ስነ ልቦናዊ  ምንጮች፡፡ እነዚህም የሚከተሉትን ሊያጠቃልል ይችላል፡-
በስራ ቦታ በሚፈጠር የሥራ ጫና
የሥራ አሰራር ግልፅነት ማጣት
ከሚወዱት ሰው ጋር የሚፈጠር ችግር
መሰረታዊ የኢኮኖሚ ግዴታዎችን መወጣት አለመቻል፡- ለምሳሌ የቤት ኪራይ፣ አስቤዛ፣ ወርሃዊ የመብራት ክፍያ ወዘተ…
ለአዳዲስ ነገሮች መዘጋጀት፡- ለምሳሌ ልጅ መወለድ፣ አዲስን ስራ መያዝ
የትራፊክ መጨናነቅ
ከፍተኛ ድምፅ
ህመም
ክፍተኛ የአየር ሁኔታ፡- ለምሳሌ ከባድ ሙቀት ወይም ከባድ ቅዝቃዜ
አካላዊ ህመም፣እንቅልፍ ማጣት፣ከመጠን ያለፈ አልኮል መጠጣትና ሲጋራ ማጨስ በሰውነት ላይ የሚፈጥሩት ጫና ወዘተ ናቸው
ቲምና ፔተርሰን (Timm and Peterson) የተባሉ ምሁራን  በተለይ በሥራ አካባቢ የጭንቀት ምንጮች የሚላቸውን  እንደሚከተለው ይዘረዝራሉ።
ውጤታማ ያልሆነ ተግባቦት (Communications)
አግባብነት የጎደለው የመስሪያ ቤት አሰራር
ከመጠን በላይ የሆነ የመረጃ ብዛት
ወጥ ያልሆነ የሥራ አስኪያጆች ወይም የመሪዎች ባህሪ
ከመጠን ያለፈ የስራ ብዛት ወይም ጫና
አዲስ ሥራ መግባት
የግል ችግሮች
ጭንቀትን የሚዘሩ ግለሰቦች- በንግግራቸው ሁሉ ጭንቀት የሚፈጥር ወሬን የሚያወሩ (Stress carriers ይባላሉ)
የ ድርጅቶች ደሞዝ፣ፖሊሲ እና የስራ አካባቢ(working conditions)
የሥራ ቦታዎች ከፍተኛ ሙቀት ወይም ቅዝቃዜ፣ ከፍተኛ ብርሃን ወይም ድንግዝታ ለጭንቀት መነሻዎች እንደሆኑ በፃፉት መፅሃፍ ላይ ይገልፃሉ፡፡
የጭንቀት ውጤቶች ምንድናቸው?
የሰውነት ድካም
ከፍተኛ የራስ ምታት
ብስጭት
የምግብ ፍላጎት መዛባት
የማስታወስ ችሎታ መቀነስ
ለራስ የሚሰጥ ዋጋ ወይም ክብር መቀነስ(low self-esteem)
ከማህበራዊ ህይወት መገለል
የ ደም ግፊት መጨመር
ትንፋሽ ማጠር
የወሲብ ፍላጎት መቀነስ
የእንቅልፍ መዛባት
የጨጓራና አንጀት ስርዓት መዛባት  ወዘተ
ከእነዚህም በተጨማሪ ጭንቀት  የልብ ህመምን፣ የቆዳ ችግርን(skin disorders) እና ሜታቦሊዝምን (በሰውነታችን ውስጥ የሚካሄዱ ኡደቶችን)የማዛባት አቅም አለው ተብሎ ይታመናል፡፡ በተጨማሪም ለስነልቦናዊ ቀውሶች ለምሳሌ፡- ለፍርሃትና ለድብርት ይዳርጋል፡፡ ጭንቀት ስነልቦናዊ ችግር ነው ቢባልም አካላዊ ተፅእኖን ይፈጥራል፡፡
ጭንቀትን ለመቀነስ ምን ማድረግ አለብን ?
ከላይ የተጠቀሱት  ምሁራን ለጭንቀት መላ ይሆናሉ ያሉትን መፍትሄዎች እንደሚከተለው ዘርዝረዋል፡-
ለአፍታ ዞር ይበሉ፡- ጭንቀት ከፈጠረብዎ ሁኔታ ወይም ሌላ ምንጭ ዞር ይበሉና የማሰቢያና የማሰላሰሊያ ጊዜ ይውሰዱ፡፡
ያውሩት፣ይናገሩት፡-ለቅርብና ለሚያምኑት ሰው የጭንቀትዎን ስሜት  ይናገሩ፡፡ ባወሩ ቁጥር ይቀልልዎታል፡፡
ወጣ ብለው የሚወዱትን ይጫወቱ፡- የእግር ጉዞ ያድርጉ፣ ደረጃዎችን ወደ ላይና ወደ ታች ይውጡ፡፡
አንዳንዴ እጅ ይስጡ፡- ለምሳሌ እርስዎና ባለቤትዎ ወይም አለቃዎ “ይሄ ነው ትክክል ያኛው ነው ትክክል ” እያሉ ሙግት ከገቡና ጉዳዩ ብዙ ለወጥና ተፅዕኖ የማያመጣ ከሆነ ችላ ይበሉት፤ አንዳንዴ እያወቁ ይተውት፡፡
ለሌሎች መልካም ነገር ያድርጉ፡-በከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ ሲገቡና ሃዘን ውስጥ ሲሆኑ ችግረኞችን በመርዳትና ልገሳ በማድረግ ይሳተፉ፤ ቀለል ይልልዎታል፡፡
በአንድ ጊዜ አንድን ነገር ይስሩ፡- ሁሉንም ነገር በአንድ ጊዜ ለመስራት መሞከር ጭንቀትን ስለሚያባብስ እንደ ስራዎቹ ጠቃሚነትና አስቸኳይነት ቅደም ተከተል  በማሲያዝ  በአንድ ጊዜ አንድን ነገር ይስሩ፡፡
የታላቁን ሰው ፍላጎት አድብ ግዛ ይበሉት፡-አንዳንዴ የራስዎንም ሆነ የሌሎች ሰዎችን ችግር በሙሉ ራስዎ መፍታት እንደሚችሉ ማሰብዎ “በውስጥዎ ያለው የሃሰተኛው ትልቅ ሰው urge of superman” ምክር ነውና አድብ ግዛ ይበሉት፡፡ እርስዎ የሁሉንም ሰው ችግር ፈቺ አይደሉም፡፡
ትችትን መቋቋም ይለማመዱ፡- አንዳንድ ሰው ትንሽ ትችት እንቅልፍ ትነሳዋለች፡፡ በተጨማሪም ሌሎችንም ከመተቸት ይቆጠቡ። ቶማስ ፍሬድማን የ “ The world is flat” ፀሃፊ በዚህ አለም አንድ መንደር በሆነችበት ግሎባላይዜሽን ዘመን ለትችት ቆዳህን አወፍር (Make your skin thick) ብሎ ይመክራል፡፡
ለሌሎች ራስህን አስገኝ፡- ሰዎች ሲፈልጉህ ተገኝላቸው፡፡ ብቸኝነት የጭንቀት ምክኒያትም ሊሆን ስለሚችል፡፡
ራስህን ለማዝናናት ጊዜ ውሰድ፡-ዘና ማለት፣መጫወት፣ አዳዲስ ነገሮችን መጎብኘት መንፈስን ያድሳል፣ ጭንቀትንም ይቀንሳል፡፡
ቆፍጣና ሁን፡- በቀን ወስጥ የምትሰራውን፣ የምትሄድበትን ሥፍራ፣ የምታገኘውን ሰው በትክክል ለይተህ በማወቅ ዝርክርክነትን አስወግድ።
ስብዕናህን ፈትሽ፡- ጭንቀት ውስጥ የሚከትህንና የማይከትህን ነገሮች ለይተህ በመረዳት ራስህን ጠብቅ፡፡
ከላይ ከተጠቀሱት በተጨማሪ ጭንቀትን ለመቀነስ ቴክኒኮችን ማወቅና አስተሳሰብን መለወጥ አስፈላጊ ነው፡፡ ይህም በሥልጠናና በባለሙያ የካውንሰሊንግ አገልግሎት  ሊገኝ ይችላል፡፡
ለዛሬ ሁለት ቴክኒኮችን ብቻ  እንመልከት(በርካታ ቴክኒኮች እንዳሉ መገንዘብ ያስፈልጋል)፡-
አንደኛው በእንግሊዝኛው ምህፃረ ቃል ABCDE ተብሎ የሚጠቀሰው ነው፡፡ ይህ ቴክኒክ አልበርት ኤሊስ (Albert Ellis) በተባሉ የስነልቦና ባለሙያ የተገኘ ዘዴ ነው፡፡ አልበርት ኤሊስ ሰዎች ወደ ጭንቀት የሚገቡት አግባብ ያልሆነ አስተሳሰቦችና እምነቶች  (Irrational beliefs and thoughts) ሲጠናወቷቸው ነው ብለው ያምናል:: ለምሳሌ ሰው ሁሉ ይጠላኛል፣ ሰው ሁሉ ይወደኛል፣ ከሰው ሁሉ ተቀባይነትን ማግኘት አለብኝ፤ በምሰራው ስራ ሁሉ መሳሳት የለብኝም ወዘተ የሚሉ እምነቶችና አስተሳሰቦች ለጭንቀት እንደሚዳርጉ ያሰምሩበታል። እኚህ ሰው እንደሚሉት አሉታዊ ነገሮችን አጋኖ ማየት(Awfulising)፤ ጥቁርና ነጭ እሳቤ(Black and White thinking) (ይህ እንግዲህ አንድን ነገር ጥሩ ወይም መጥፎ ብሎ መመደብና በውስጡ ሊኖር የሚችለውን የተወሰነውን ጥሩ ነገር አለማየት ነው)፣ጠቅላይ እሳቤ (Over generalizing)-ሁልጊዜ፣ሁሉም ሰው፣ በፍፁም ወዘተ የሚሉ ቃላትንና ሃሳቦችን መጠቀም፤ የማይመለከተንን ነገር ከራሳችን ጋር አቆራኝቶ ማየት (Personalizing)፤ በሁኔታዎች ውስጥ አሉታዊን ነገር ብቻ መርጦ ማየት(Filtering)፣ ይህንን አስቦ ነው ብሎ ያለምንም ማስረጃ ድምዳሜ ላይ መድረስ (Mind reading)፣ሰዎችን መተቸትና መውቀስ (Blaming)፣ለራስ ስያሜ መስጠት ለምሳሌ ደካማ ነኝ፤ዋጋ ቢስ ነኝ ወዘተ ማለት (Labeling) አግባብ ላልሆኑ አስተሳሰቦች ምክኒያት ናቸው ይሉናል፡፡
የ ABCDE ቴክኒክን ተንትነን ለማየት እንሞክር
Antecedent(Activating event, Stimulus)፡ ይህ ማለት ጭንቀትን የሚቀሰቅሰው ሁኔታ ወይም ነገር ነው(ተንኳሽ እንበለው)፡፡ ይህ ተንኳሽ  የኛን ምላሽ (Response) ይጠይቃል። ለምሳሌ ከስንት አንድ ቀን ቀጠሮ ብናረፍድ ጭንቀት ሊፈጠርብን ይችላል፡፡ በዚህ ምሳሌ መሰረት ጭንቀትን የሚፈጥርብን ጉዳይ ማርፈዳችን ነው ማለት ነው፡፡
Belief-our cognition about the situation፡- ይህ እንግዲህ ስለ ተንኳሹ ያለን ሃሳብና እምነት ነው፡፡ ለምሳሌ ማርፈዴ ያለኝን ተቀባይነት ያሳጣዋል፣ በምንም አይነት ምክኒያት ቢሆን ማርፈድ አሳማኝ አይደለም ወዘተ የሚል እምነት ማለት ነው፡፡
Consequences-the way that we feel and behave፡ ይህ ውጤት ነው - ጭንቀታችን፡፡ ይህ ምን  ባህሪ ይፈጥራል? ቶሎ ለመድረስ አላግባብ ጣልቃ እየገባን መኪናችንን መንዳትን፣ በእጃችንም በአንደበታችንም የተንቀረፈፈ የመሰለንን ሾፌር መስደብ፣መቆጣት፤ ከአስፋልት ወጥቶ በእግረኛ መንገድ መንዳት  ወዘተ ማለት ነው፡፡ እዚህ ላይ አልበረት ኤሊስ ይሞግታሉ “ያስጨነቀን ማርፈዳችን ነው ወይስ ስለ ማረፈድ ያለን አስተሳሰብና እምነት ነው?” አሳቸው እንደሚሉት፤ ውጤቱን የፈጠረው ማርፈዳችን(stimuls ) ሳይሆን ስለ ማርፈድ ያለን አስተሳሰብና እምነት ነው ባይ ናቸው፡፡
Dispute is the process of challenging the way we think about situations: ይኸኛው አስተሳሰባችንን የምንሞግትበት ዘዴ ነው። እሳቸው አግባብነት የሌለውን አስተሳሰብና እምነት መሞገት ያስፈልጋል ይላሉ፡፡ ለምሳሌ ከላይ የጠቀስነውን ማርፈድ ብንወስድ እምነታችንን ስንሞግተው እንደሚከተለው ይሆናል፡፡ “ ብዙ ጊዜ በሰዓቱ የምገኝና ቀጠሮ አክባሪ የሆንኩ ሰው ነኝ፡፡ አንድ ዛሬን ባረፍድ ተቀባይነቴን አያሳጣም”፣ “ለማርፈዴ ምክኒያት የሆነኝ የትራፊክ መጨናነቅና ያልጠበቅሁት የመንገዶች መዘጋጋት ነው፡፡ ስለዚህ በቂ ምክኒያት ሊሆን ይችላል፡፡” እነዚህን ምክኒያቶች በማሰብ ነባሩን ሃሳብ መሞገት እንደሚገባ ይጠቁማሉ፤ አልበርት ኤሊስ፡፡
Effect: ይሄ አዲሱ ውጤት ነው። አስተሳሰባችንን ከሞገትነውና በአዲስ አስተሳሰብ ከተካነው በኋላ የሚፈጠር ባህሪ ነው፡፡ የላይኛውን ምሳሌ ብንከተል ተረጋግቶ መንዳት፤ ተራ መጠበቅ፤ በተፈቀደው አስፋልት መንዳት ወዘተ ማለት ነው፡፡ በነገራችን ላይ ሃሳብ ስሜታችን እና ባህሪያችን ላይ ተፅእኖ ይፈጥራል፡፡
በሁለተኛ ደረጃ የሶቅራጠስን ቴክኒክ እንመልከት፡- የጥንቱ የግሪክ ፈላስፋ ሶቅራጠስ አስጨናቂ ሁኔታዎች ሲፈጠሩ የሚጠይቃቸውን  የሚከተሉትን አምስት ጥያቄዎች መጠየቅ ይጠቅማል፡፡
ተጨባጩ ነገር ምንድነው?  ስለዚህ ነገር ያለኝ የኔስ  የግል እሳቤ?
የግል እሳቤዬን  የሚደግፍ ማስረጃ አለ?
የግል እሳቤዬን የሚቃረን ማስረጃስ?
የአስተሳሰብ ስህተት ፈፅሜያለሁ?
ስለ ተፈጠረው (ስለ ተጨባጩ) ሁኔታ ምን ማሰብ አለብኝ?
ነገሩ የግል እሳቤን የሚያጠናክር ማስረጃ ካለው(ተ.ቁ 2.2) ለችግሩ መላ መፈለግ ያስፈልጋል። ከእምነቴ ተቃራኒ  ከሆነ(ተ.ቁ 2.3) መጨነቅ ለማያስፈልገው ነገር ጊዜዬን እያባከንኩ ወይም ለጭንቀት ውጤቶች ራሴን እየዳረግሁ ነው ማለት ነው፡፡ የሶቅራጠስ ቴክኒክ የነገሮችን ወይም የሁኔታዎችን ተፅእኖ የምንፈትሽበትና የእርግጠኝነት ምላሽን የምንፈልግበት ነው፡፡ በነገራችን ላይ ዴል ካርኒጊ፤ አብዛኛው ሰው የሚጨነቀው ገና ባልደረሰብት ችግር ነው የሚል አስተሳሰብ ነበረው።
በመጨረሻም እንድ ማወቅ የሚገባን ነገር አለ፡- እንዳንድ ነገሮችንና ሁኔታዎችን መቆጣጠር እንችላለን። ይህንን ፅሁፍ ማዘጋጀትና አለማዘጋጀት በኔ ቁጥጥር ስር ነው፡፡ ከፈለግሁኝ አዘጋጀዋለሁ ካልፈለግሁኝ አላዘጋጀውም፡፡
ስለ ፈለግሁኝ አዘጋጀሁት፡፡ በአንዳንድ ነገሮች ወይም ሁኔታዎች  ደግሞ ተፅእኖ መፍጠር እንችላለን ነገር ግን ልንቆጣጠራቸው አንችልም፡፡ ለምሳሌ በቡድን በሚሰሩ ስራዎች እርስዎ የሚያምኑበትን ነገር ተግባራዊ እንዲሆን የስራ አመራሩን ተፅኖ ሊፈጥሩበት ይችላሉ  እንጂ ውሳኔውን  በግልዎ ሊቆጣጠሩት አይችሉም። አንዳንድ ነገሮችን ደግሞ መቆጣጠርም ሆነ ተፅእኖ መፍጠር አይቻልም። ስለዚህ ሁኔታውን መቀበል ወይም በሁኔታው ውስጥ ውጤታማ ሆኖ ለመኖር መወሰን ነው የሚጠበቅብዎ፡፡ ለምሳሌ የእርስዎ የቅርብ ሰው በሞት ቢለይ ወይም ፈፅሞ እርስዎን ላለማግኘት ወስኖ ከእርስዎ መለየት  ቢቆርጥ የሚቀይሩት ጉዳይ ስላልሆነ መቀበል እንዲሁም በተፈጠረው ሁኔታ ውስጥ ራስን አዘጋጅቶ መኖር ያስፈልጋል።
 አብዛኛው ሰው መቆጣጠር የሚገባውን ነገር ለሌሎች ተፅእኖ አሳልፎ ሲሰጥ ወይም ተቀብሎ ሲኖር፣ ወይም ተፅእኖ ማሳደር የሚገባውን ነገር ለመቆጣጠር ወይም በቸልተኛነት ሲቀበለው እና ራስን አዘጋጅቶ መኖር የሚገባውን ወይም መቀበል ያለበትን ሁኔታና ነገር ለመቆጣጠር ወይም ተፅእኖ ለማሳደር ሲሞክር የጭንቀት ሰለባ የመሆኑ ዕድል የሰፋ ነው። ይህንን በአጭሩ ለማስታወስ በእንግሊዝኛው ምህፃረ ቃል CIA-Control-Influence-Accept/Adapt to ብሎ መያዝ ይጠቅማል፡፡
አንዳንዱን ነገር Control እናደርጋልን፤ አንዳንዱን influence  ነው የምናደርገውን አንዳንዱን ደግሞ Accept/Adapt to ነው ማድረግ የሚገባን፡፡
ቸር እንሰንብት
(ፀሐፊውን በሚከተለው የኢ-ሜይል አድራሻው ሊያኙት ይችላሉ This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. )

Published in ዋናው ጤና

የተቃዋሚዎችን ጥርስ ከማውለቅ የመኪናቸውን ጎማ ማስተንፈስ!  
የብራዚልና የጀርመን ጨዋታ የ97 ምርጫን አስታወሰኝ (ዱብዕዳ!)

አብዛኞቹ የእግር ኳስ አፍቃሪዎች ሰሞኑን በብራዚል ላይ የደረሰውን ያልተጠበቀ ሽንፈት ለማመን አቅቷቸው ነው የሰነበቱት፡፡ የጀርመን ቡድን በእግር ኳስ ጥበብ ዝናዋ በናኘው ብራዚል ላይ 7 ጎሎችን አግብቶ ጉድ ይሰራታል ብሎ ማን ገመተ። (እንደ 97ቱ ምርጫ ማለት እኮ ነው!) ቢገመትማ ዱብእዳነቱ ይቀራል፡፡ አንዳንድ ሁሉ ነገር በሃርድ የሚመስላቸው  የኢህአዴግ ፍሬሽ ካድሬዎች፤ ኳስና ምርጫን ምን አገናኛቸው ብለው ሊደነፉ ይችላሉ (መደንፋት መብታቸው ነው!) እኛ ግን ምን እንደሚያገናኛቸው በእርጋታ የማስረዳት አገራዊ ሃላፊነት ተጥሎብናል፡፡ አንደኛ ሁለቱም ውድድሮች ናቸው፡፡ ሁለተኛ ደግሞ የሁለቱም ውጤት ዱብዕዳ ነው፡፡ የኢህአዴግም የብራዚልም ሽንፈት!!
በነገራችሁ ላይ በ97ቱ ምርጫ የአዲስ አበባን ውጤት አምኖ መቀበል የተሳናቸው የኢህአዴግ አመራሮች ብቻ አልነበሩም፡፡ ራሳቸው የቅንጅት መሪዎችም በዝረራ እናሸንፋለን ብለው አልገመቱም ነበር፡፡ (ለዚህ ይሆን እንዴ አያያዙን ያላወቁበት?!)
በብራዚልና በጀርመን ጨዋታ የብራዚልን ዱብዕዳ የሆነ ሽንፈት ማመን ያቃታቸው ቡድኖቹ ሳይሆኑ ደጋፊዎቹ ነበሩ (ቀላል አነቡ!) እኔ የምለው… በምርጫ መሸነፍ ያስለቅሳል እንዴ? (ያስደነፋል እንጂ አያስለቅስም!) ከአገራችን የቴሌቪዥን ተመልካቾችም የብራዚልን ሽንፈት ማመን ያቃታቸው አልጠፉም፡፡ አንዱ ጨዋታው ከተጠናቀቀ በኋላ “የእኔ ቴሌቪዥን ተሳስቶ እንዳይሆን” በሚል ጓደኛውን ደውሎ እንደጠየቀው ሰምቻለሁ፡፡ በነጋታው በጨዋታው ዙሪያ በተደረገ ጨዋታ ደግሞ “የሆነ ነገር አዙረውባቸው መሆን አለበት እንጂ…” ሲሉ አንዳንድ የብራዚል ደጋፊዎች በጀርመን ቡድን ላይ ያላቸውን ጥርጣሬ ገልፀዋል። የብራዚል የእግር ኳስ ባለሙያዎችና አንጋፋ ተጫዋቾች ግን ሽንፈቱን A blessing in disguise ነው ብለውታል። (ሳይደግስ አይጣላም እንደማለት!) “ጥሩ አጋጣሚ ነው፤ ራሳችንን በቅጡ እንድንፈትሽ ዕድል ሰጥቶናል” ሲሉም ተፅናንተዋል። እኔ ግን “አያድርስ” ብየዋለሁ - የብራዚልን ያልተጠበቀ ሽንፈት። ፓርቲዎች በምርጫ ሲሸነፉ ሰማይ የተደፋባቸው ከሚመስሉ It is a blessing in disguise ማለትን ቢለምዱ መልካም ነበር፡፡ (ክንዳቸውን ሳይንተራሱ?)   
አሁን ደግሞ ወደ ሌላ ጨዋታ እንግባ። ዚምባብዌ ውስጥ ነው አሉ - በአዛውንቱ የሙጋቤ አገር፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ በጥባጭ (Rogue) ዝሆኖች ከተፈቀደላቸው የመኖርያ ክልል በመውጣት የነዋሪዎችን ማሳና ጎጆ እየደረማመሱት ይሄዱ ጀመር። በፖለቲካ ቋንቋ “ነውጠኛ” ሆኑ ማለት ነው- ዝሆኖቹ፡፡ የዚምባቡዌ መንግስት ደግሞ ለ“ነውጠኛ ተቃዋሚዎች” እንጂ ለነውጠኛ ዝሆኖች ምላሽ ሰጥቶ አያውቅም፡፡ እናም ትንሽ ታገሳቸው። ዝሆኖቹ ግን መደረማመሱ ተመቻቸው መሰለኝ ደጋግመው ወደ ገበሬዎቹ ማሳ በመመላለስ የከፋ ውድመት አደረሱ፡፡
ይሄኔ መንግስት በነውጠኛ ተቃዋሚዎች ላይ መውሰድ የለመደውን እርምጃ ሊወስድባቸው የጦር መሳሪያውን መወልወል ጀመረ - ቃታ ሊስብ፡፡ የማታ ማታ ግን አማካሪ አይጥፋ ሃሳቡን ቀየረ፡፡ እርምጃው በዓለም አቀፍ የዱር እንስሳት መብት ተሟጋቾች ዘንድ መብጠልጠልንና መወንጀልን ስለሚያስከትል ሌላ መላ ተዘየደ - በአማካሪዎቹ ሃሳብ አመንጭነት። እናም የዚምባብዌ መንግስት በተለያዩ ድረ-ገፆችና ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ተከታዩን መልእክት አሰራጨ፡-
“በመላው ዓለም ለዱር እንስሳት መብት ተሟጋች ነን የምትሉ ወገኖች ሁሉ፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዱርዬ ዝሆኖች ከመኖሪያቸው ክልል ወጥተው የህብረተሰቡን ህይወት እየረበሹ ነውና… በፍጥነት ደርሳችሁ በራሳችሁ ትራንስፖርት ሰብስባችሁ በመውሰድ ለምትፈልጉት ጉዳይ (ለሰርከስ ይሁን ለሌላ) መጠቀም እንደምትችሉ እያሳወቅን፤ ይሄን በአስቸኳይ ባታደርጉ ግን በዝሆኖቹ ላይ የማያዳግም እርምጃ ለመውሰድ እንደምንገደድ እንገልፃለን”
መረጃው በተሰራጨ 24 ሰዓት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ከዱር እንስሳት መብት ተሟጋች ድርጅቶች አንዱ በፈጣን አውሮፕላን ዚምባብዌ ገጭ አለ። ወዲያው ከመንግስት ጋር ተደራድሮ ዝሆኖቹን ሰበሰበ፡፡ እድሜ ለመብት ተሟጋቾች! የዚምባብዌ ዝሆኖች “ነውጠኛ” በሚል ተፈርጀው በጅምላ ከመረሸን ተረፉ፡፡ የበለጠ ከሚያውቃቸው የአፍሪካ መንግስት ይልቅ በዱር እንስሳትነታቸው (በመንፈስ እንደማለት ነው) ብቻ የሚያውቃቸው ምዕራባዊ የመብት ተሟጋች ድርጅት ህይወታቸውን ታደጋቸው፡፡ ለነውጠኞቹ ዝሆኖች  ተወልውሎ የነበረው የጦር መሳሪያ ለተቃዋሚዎች (ለስልጣን ተቀናቃኞች ማለት ነው!) ተብሎ ተቀመጠ። (ለማስፈራርያ እኮ ነው!)
ከላይ የቀረበውን ታሪክ ያወጋኝ አንድ የቅርብ ወዳጄ ነው - አነበብኩት ብሎ፡፡ እኔ ታዲያ ወዲያው አንድ  ሃሳብ ብልጭ አለልኝ፡፡ ዶሮ ብታልም ጥሬዋን እንዲሉ… ዝሆኖቹ ከጅምላ ጭፍጨፋ የዳኑበትን ምስጢር ለአፍሪካ ተቃዋሚዎች ለምን አንጠቀምበትም አልኩኝ - ለራሴ፡፡ ትንሽ በውስጤ ካብሰለሰልኩት በኋላ ግን ይኸው ለናንተም አቀረብኩት፡፡ በዝሆኖቹ ታሪክ ኢንስፓየር ሆኜ ያመነጨሁትን አዲስ ሃሳብ!! ለየትኛውም የአፍሪካ መንግስት ከረባሽ ዝሆኖችና ከተቃዋሚዎች የቱን ትመርጣለህ የሚል ጥያቄ ቢቀርብለት፣ ረባሽ ዝሆኖችን እንደሚመርጥ ሳይታለም የተፈታ ነው። (ስልጣን መነቅነቅና ማሳ መደርመስን ምን አገናኛቸው?!)
እናንተ ስለአፍሪካ መንግስታት ያላችሁን ግንዛቤ በትክክል ባላውቅም እኔ ግን በአንድ ነገር እርግጠኛ ነኝ፡፡ የአፍሪካ መንግስታት በምዕራባውያን የኢኮኖሚ ተፅዕኖ ስር ባይሆኑ ኖሮ፣ እስካሁን ተቃዋሚዎች እንደ ዳይኖሰር ከምድረ ገፅ መጥፋታቸው አይቀርም ነበር፡፡ ከተቃዋሚዎች ቀጥሎ እንደ ዳይኖሰር የሚጠፋው ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? “ምርጫ” የሚለው ቃል ነው። ይሄን ቃል ተከታትለው ከአፍሪካ ምድር የሚጠፉት “ዲሞክራሲ” እና “የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት” የሚሉ ቃላትና ሃረጎች እንደሚሆኑ ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡
ወደ ዋና ጉዳያችን ስንመለስ … ለአፍሪካ ተቃዋሚዎች ብዬ ያመነጨሁት ሃሳብ ለአፍሪካ መንግስታትም በእጅጉ የሚበጅ መሆኑን አስረግጬ እናገራለሁ፡፡ በነገራችሁ ላይ በአብዛኞቹ የአፍሪካ አገራት ተቃዋሚዎች በገዢው ፓርቲ ላይ የሚነሱትና “ድር ቢያብር አንበሳ ያስር” ብለው ህብረት የሚፈጥሩት በምርጫ ዋዜማ ነው፡፡ ያኔ መንግስት ጠባይ ያለውን ሰብስቦ ወህኒ ያጉራል። ትዕቢት ትዕቢት የሚለው ካለ ደግሞ ጥርሱን ሊያወልቀው ይችላል፡፡
 እኔ የምለው…ባለፈው ሳምንት የአንድነት አመራር አባልን ጥርስ ያወለቁት የደህንነት ኃይሎች ናቸው የተባለው እውነት ነው እንዴ? (ጥያቄ ነው!) ከመንግስት ወገን ማረጋገጫ አልተሰጠም ብዬ እኮ ነው (መች ተሰጥቶ ያውቃል እንዳትሉኝ!) ባለፈው ምርጫ የኢህአዴግ ካድሬዎች የአንድነትን የቅስቀሳ መኪና ጐማ አተነፈሱ ተብለው መወንጀላቸውን ሰምቼ ነበር። ከራሳቸው ከአንድነቶች፡፡ ነገርዬው ተገቢ ባይሆንም ጥርስ ከማውለቅ ግን ሺህ ጊዜ ይሻላል፡፡ (ማውለቅም ማተንፈስም ቢከለከል ጥሩ ነው!)
እናላችሁ ---- የባሰባቸው የአፍሪካ መንግስታት ዓይን ከማጥፋትም ወደ ኋላ አይሉም (ምን ነካችሁ--- ነገርዬው ሥልጣን እኮ ነው!) ይሄ ደግሞ ምዕራባውያኑ  ጆሮ መድረሱ አይቀርም፡፡፡ የአፍሪካ መንግስታት እቺን እቺን ፈፅሞ አይፈልጓትም፡፡ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ነን ባዮች ሪፖርትም ይከተላል፡፡ ከዚህ ሁሉ ጣጣ ያድናል ባይ ነኝ አዲሱ የመፍትሄ ሃሳቤ፡፡ እናላችሁ… የአፍሪካ መንግስት በምርጫ ዋዜማ ላይ ልክ ለረባሾቹ ዝሆኖች ያሰራጩት አይነት መልእክት በተለያዩ ሚዲያዎች ያሰራጫሉ - ለሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች፡፡ እንዲህ ሊል ይችላል፤ መልእክቱ -
“በመላው ዓለም የሰብአዊ መብት ተሟጋች ነን የምትሉ ወገኖች ሁሉ፤ በዚህች አገር ላይ የሚገኙ ነውጠኛ ተቃዋሚዎችን በራሳችሁ ትራስፖርት ሰብስባችሁ በመውሰድ (ለሰርከስ ይሁን ለሌላ) ለምትፈልጉት ጉዳይ መጠቀም የምትችሉ መሆኑን እያሳወቅን፣ ይህን የማታደርጉ ከሆነ ግን በነውጠኞቹ ተቃሚዎች ላይ ተገቢ ያልነውን እርምጃ ለመውሰድ እንገደዳለን”
ይሄ ማሳሰቢያ በተሰራጨ በአጭር ጊዜ ውስጥ እነ አምነስቲና ሂዩማን ራይትስዎች በፍጥነት ደርሰው የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትንና ደጋፊዎችን ሰብስበው ከአጥፊነትም ከመጥፋትም ይታደጓቸዋል - እንደ ረባሾቹ ዝሆኖች ማለት ነው፡፡
በዚህም የአፍሪካ ተቃዋሚዎች እንደ ዳይኖሰር ከምድረ ገፅ ከመጥፋት ይድናሉ - በሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ጠባቂነት፡፡ የአፍሪካ መንግስታትም በየአራትና አምስት ዓመቱ ለምእራባውያን እርዳታ ሲሉ  ሲያደርጉት ከነበረው የይስሙላ ምርጫ ይገላገላሉ። (እፎይ ብለው የሰላም እንቅልፍ ይለጥጣሉ!) በሆነ ተዓምር ተቃዋሚዎች ከስልጣን ነቅንቀው ይጥሉን ይሆን? ከሚል ራስ ምታት ይገላገላሉ፡፡ (Win/Win Situation ይሏል ይሄ ነው!)
ወዳጆቼ፤ሌላው ሁሉ መፍትሔ ተሞክሮ ስላልሰራ ይሄ ደሞ ይሞከራ!! ተቃዋሚዎችን ከመጥፋት እንታደጋቸው፡፡

Page 10 of 16