“የታሰሩት የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ይፈቱ” የሚል ተቃውሞ ትናንት ከቀትር በኋላ በተካሄደበት የታላቁ አንዋር መስጊድ አካባቢ በርካታ ፖሊሶች ተሰማርተው የዋሉ  ሲሆን፤ ለሰዓታት በዘለቀው ግርግርና ረብሻ የተኩስ ድምጽ የተሰማ ቢሆንም የደረሰው ጉዳት እስካሁን በዝርዝር አልታወቀም፡፡ ቁጥራቸው ያልታወቁ ሰዎች በፖሊስ ተይዘው ሲወሰዱ ታይቷል፡፡
ተቃውሞና ግርግር የተፈጠረው የጁምዓ ስግደት ከመጠናቀቁ በፊት እንደሆነ የተናገሩ የአይን እማኞች፤ ቆመጥ የያዙ ፖሊሶች ተሰማርተው እንደነበርና በርካቶች ድብደባ እንደደረሰባቸው ገልፀዋል፡፡
በተክለሃይማኖት አደባባይ እና ከፒያሳ ወደ መርካቶ የሚወስዱ መንገዶች ለእግረኞችና ለተሽከርካሪ ተዘግተው የነበረ ሲሆን፤ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ለእግረኞች መከፈቱን የተናገሩ የአካባቢው ሰዎች፤ ግርግሩ ግን ወዲያው አልቆመም ብለዋል፡፡
“የታሰሩት የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ይፈቱ” ከሚለው እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ “ድምፃችን ይሰማ” በተሰኘው ድረገፅ የተቃውሞ ጥሪ ሲተላለፍ እንደሰነበተ ምንጮች ገልፀዋል። አምናም በተመሳሳይ የረመዳን የጾም ወቅት፣ በሦስት የአዲስ አበባ መስጊዶች ሦስት ሰፋፊ ተቃውሞዎች መካሄዳቸው ይታወሳል፡፡

Published in ዜና

ተከሳሾቹ ከግንቦት ሰባትና ከኦነግ ጋር ግንኙነት እንዳላቸው በመዝገቡ ተገልጿል

      በፌደራል ፖሊስ ከታሰሩ አራት ሳምንት የሆናቸው ስድስት የድረገጽ ፀሐፊዎች (ጦማሪዎች) እና ሦስት ጋዜጠኞች ትናንት በአቃቤ ህግ የሽብር እና የአመጽ ክስ የቀረበባቸው ሲሆን፤ በክሱ ላይ አስተያየት ለመስጠት ለሐምሌ 28 ቀን ተቀጠሩ፡፡ “ዞን 9” በሚል ስያሜ የሚታወቁት ስድስቱ ጦማሪዎች እና ሦስቱ ጋዜጠኞች፤ በድብቅ (በህቡዕ) ተደራጅተው ሲሰሩ ቆይተዋል በማለት የገለፀው አቃቤ ህግ፤ ህቡዕ የተባለው ድርጅት “ዞን 9” ይሁን ሌላ በስም አልጠቀሰም፡፡ የግል የመልእክት ልውውጦችን በሚስጥር የመጠበቅ ዘዴ በአገር ውስጥና በውጭ ስልጠና ወስደዋል በማለትም አቃቤ ህግ ሁሉንም ተከሳሾች ጠቅሷል፡፡ ስልጠናዎቹ በማን እንደተሰጡ ባይገለጽም፤ ፀሐፊዎቹና ጋዜጠኞቹ በአለም አቀፉ የፕሬስ ነፃነት ተቋም (አርቲክል 19) አማካኝነት፤ ለጋዜጠኞች የሚዘጋጅ የመረጃ አጠባበቅ ስልጠና ወስደዋል ተብሎ ሲዘገብ ከነበረው ስልጠና ጋር የሚገናኝ መሆን አለመሆኑ በግልጽ አልታወቀም፡፡ አቃቤ ህግ በስም ዝርዝር ባቀረበው ክስ፤ ተከሳሾቹ ተቃውሞና አመጽ እንዴት ማካሄድና መቀስቀስ እንሚደቻልም ሰልጥነዋል ብሏል፡፡
በተከሳሾቹ ኮምፒዩተር፣ ፍላሽ ዲስክ ወይም በመኖሪያ ቤት የተለያዩ የፖለቲካ ጽሑፎች እንደተገኙ የጠቀሰው አቃቤ ህግ፤ በግንቦት ሰባት ወይም በኦነግ የተሰራጩ ጽሑፎችን አግኝቼባቸዋለሁ ብሏል፡፡ ጽሑፎቹ ከተከሳሾቹ የጋዜጠኝነት ሙያ ጋር የተያያዘ መሆን አለመሆን በእርግጠኝነት ለማወቅ እንዴት እንደሚቻል በክሱ ውስጥ ባይጠቀስም፤ አቃቤ ህግ ጽሑፎቹ የግንቦት ሰባት አስተሳሰብና እቅድ መቀበልን እንደሚያሳዩ ያመለክታል ብሏል፡፡
በዘጠኙ ታሳሪዎች እና በውጭ አገር በምትገኘው ሶልያና ሽመልስ ላይ የቀረበው ክስ ተመሳሳይ ቢሆንም፤ ሶልያና እና ሌሎች ሦስት ተከሳሾች በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ ከግንቦት ሰባት ጋር ግንኙነት ፈጥረዋል ተብሏል፡፡ በአንድ ተከሳሽ ላይ ደግሞ፤ ለአመጽ በሚውሉ ተቀጣጣይ ነገሮች ላይ ስልጠና ወስዷል የሚል ሃሳብ በክሱ ውስጥ ተካትቷል፡፡ አቃቤ ህግ በአስር ገጽ ካቀረበው ክስ ጋር፣ ማስረጃ ይሆኑኛል የሚላቸው በመቶዎች የሚቆጠሩ የጽሑፍ ገፆችን አያይዞ አቅርቧል፡፡ ተከሳሾችና ጠበቆች በአቃቤ ህግ በቀረበው ክስ እና የማስረጃ ሰነዶች ላይ አስተያየት ለመስጠት ለሐምሌ 28 ቀን ቀጠሮ ሰጥቷል - ከፍተኛ ፍ/ቤት፡፡  
የተከሳሾች ጠበቆች በበኩላቸው፤ በፀረ ሽብር አዋጁ አንቀፅ 3 ከ1-6 ከተዘረዘሩት ወንጀሎች አንዱንም ስላልፈፀሙ ዋስትና የሚያስከለክል ጉዳይ የለም፣ ቋሚ አድራሻ አላቸው፣ ከዚህ በፊት በዋስ ተለቀው አልቀርብም ያሉበት ሁኔታ ስለሌለ የዋስትና መብታቸው ተከብሮ ጉዳያቸውን ይከታተሉ በሚል ተከራክረዋል፡፡
በተለይም የ9ኛ ተከሳሽ የኤዶም ካሳዬ ጠበቃ ዶ/ር ዳንኤል ለገሰ፤ ደንበኛዬ የተከሰሰችበት ሁኔታ በጸረ-ሽብር አዋጁ አንቀፅ 3 ከተዘረዘሩት ውስጥ የፈፀመችው የሽብር ድርጊት ስለሌለ ዋስትና መከልከሏ ከህገ መንግስቱ ጋር የሚጣረስ በመሆኑ ለፌደራል ህገ መንግስት አጣሪ ጉባኤ ጉዳዩ ይላክልኝ ሲሉ ፍ/ቤቱን የጠየቁ ሲሆን አቃቤ ህግ ማሰብ፣ ማሴር፣ በህቡዕ መደራጀት የሚሉት ክሶች በፀረ-ሽብር አዋጁ ተካትተዋል፣ በፀረ ሽብር አዋጁ የተከሰሰ ሰው ዋስትና ተከልክሎ በእስር ይቆይ ስለሚል ጉዳዩን ወደ ህገ መንግስት አጣሪ ጉባኤ ውሰዱልኝ የሚለው መከራከሪያ ህጋዊ መሰረት የለውም ሲል ተከራክሯል፡፡ ጠበቃው አመሃ መኮንን በበኩላቸው፤ “ተደራጁ - አሰቡ” የሚባለው ጉዳይ መብታቸውን ተጠቅመው ተደራጁ እንጂ የፈፀሙት ወንጀል የለም፣ ዞን ዘጠኝም ቢሆን በተወካዮች ምክር ቤት አሸባሪ የተባለ ቡድን አይደለም፤ ስለዚህ በሽብር አዋጁ ስለተከሰሱ ብቻ ዋስትና አያስከለክላቸውም ብለዋል፡፡ ፍ/ቤቱ ግራ ቀኙን ካዳመጠ በኋላ ዋስትናን በተመለከተ የተካሄደው ክርክር ተገልብጦ የመዝገቡ አካል እንዲሆን ካዘዘ በኋላ፣ የህገ-መንግስት ትርጉምንና ዋስትናን በሚመለከት  ብይን ለመስጠት ለሐምሌ 28 ቀን ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

Published in ዜና

ለዛሬ የጠራውን ህዝባዊ ስብሰባ ሰርዟል

     የኢትዮጵያዊያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ባለፈው ዕረቡ ታስረው ካደሩ 6 አባላቱ በተጨማሪ ትላንት 8 አባላቱ ታስረው እንደዋሉ ገልፆ፤ ዛሬ ለማካሄድ ያቀደውን ህዝባዊ ስብሰባ እንደሰረዘ አስታወቀ፡፡ ህዝቡ ሳይቀሰቀስና መረጃ ሳይደርሰው የሚካሄድ ስብሰባ ግቡን መምታት አይችልም ያሉት የፓርቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደ፤ አባላቶቻችን ታስረው ቅስቀሳ ማድረግ ስላልተቻለ ስብሰባው ተሰርዟል ብለዋል፡፡ ፓርቲው በመጪው አገር አቀፍ ምርጫ፣ በሰብአዊ መብት አያያዝ፣ በወቅታዊ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ከህዝብ ጋር ለመወያየት ነበር ስብሰባውን የጠራው ተብሏል፡፡
ለህዝባዊ ስብሰባው ከሚመለከተው አካል የዕውቅና ወረቀት ከተቀበሉ በኋላ ባለፈው ረቡዕ ቅስቀሳ መጀመራቸውን የተናገሩት ፕሬዚዳንቱ፤ “የስብሰባ እንጂ የቅስቀሳ ፈቃድ የላችሁም” በሚል በቂርቆስ ክ/ከተማ ቄራ አካባቢ ፖሊስ ጣቢያ ስድስት ያህል የፓርቲው አመራሮችና አባላት ታስረው ሐሙስ ዕለት በዋስ መፈታታቸውን ገልፀዋል፡፡ አባላቱ ከተለቀቁ በኋላ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የስብሰባና ሰላማዊ ሰልፍ ማሳወቅ ክፍልና የስብሰባ ፈቃድ ኃላፊ ለሆኑት አቶ ማርቆስ ብዙነህ፤ ለቅስቀሳ ሌላ ፈቃድ ይሰጥ እንደሆነ በአካል ቀርበው መጠየቃቸውን የጠቆሙት የፓርቲው የስራ አስፈፃሚ አባል አቶ ኤርሚያስ ባልከው፤ በመስተዳደሩም ሆነ በሌላ አካል የቅስቀሳ ፈቃድ እንደማይሰጥና ቅስቀሳ ማድረግ እንደማይቻል እንደነገሯቸው ጠቁመዋል፡፡
“እውቅና ለተሰጠው ህዝባዊ ስብሰባ ቅስቀሳ ማድረግ መብት ነው” በሚል በትላንትናው እለት እንደገና ቅስቀሳ መጀመራቸውን የገለፁት አቶ ኤርሚያስ፤ በቅስቀሳ ላይ የነበሩ 8 አባላቶቻቸው እንደገና በፖሊስ ተይዘው ከታሰሩ በኋላ ማምሻው ላይ መፈታታቸውን ተናግረዋል፡፡ “ገዢው ፓርቲ የሚያካሂደው ኢ-ሰብአዊ ተግባር ለሰላማዊ ትግሉ እንቅፋት እየፈጠረብን ነው” ያሉት የፓርቲው ፕሬዚዳንት ስራ አስፈፃሚው አስቸኳይ ስብሰባ አድርጎ የአቋም መግለጫ እንደሚያወጣ ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የስብሰባና ሰላማዊ ሰልፍ ማስታወቂያ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ማርቆስ ብዙነህ በበኩላቸው፤ ፓርቲው የህዝባዊ ስብሰባ የማሳወቂያ ደብዳቤ አስገብቶ ፈቃድ ማግኘቱን ገልፀው፣ ለቅስቀሳ ፈቃድ ይሰጥ አይሰጥ ግን እንደማያውቁ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

       በጋምቤላ ክልል ለሰፈራ ፕሮግራም ከቀያቸው ከተፈናቀሉት በርካታ ሺህ ዜጐች አንዱ እንደሆኑና ወደ ኬንያ እንደተሰደዱ የገለፁ ገበሬ፤ የእንግሊዝ መንግስት ለሰፈራ ፕሮግራሙ የገንዘብ ድጋፍ በመስጠት በደል ፈጽሞብኛል በማለት ሰሞኑን በለንደን ፍ/ቤት ክስ መሰረቱ፡፡  ለኢትዮጵያ ከፍተኛ የገንዘብ እርዳታ በመስጠት በአለም ቀዳሚ ስፍራ የያዘው የእንግሊዝ መንግስት በበኩሉ፤ ለሰፈራ ፕሮግራም የሚውል ገንዘብ አልሰጠሁም በማለት ምላሽ መስጠቱን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ከአስር አመት ወዲህ በየክልሉ የሰፈራ ዘመቻዎች መካሄዳቸው የሚታወቅ ሲሆን፤ ባለፉት ሶስት ዓመታት “ከፊል አርብቶ አደር” ተብለው በሚታወቁ እንደ ጋምቤላና ሶማሌ በመሳሰሉ ክልሎች፤ ነዋሪዎችን በመንደር የማሰባሰብና የማስፈር ፕሮግራሞች ተካሂደዋል፡፡ በርካታ ነዋሪዎች ያለፈቃዳቸው በግዳጅ እየተፈናቀሉ ለችግር ተዳርገዋል የሚል ተደጋጋሚ ትችት የሚሰነዘርባቸው እነዚህ የሰፈራ ፕሮግራሞች ላይ ሂዩማን ራይትስ ዎች የተሰኘው ዓለም አቀፍ ተቋም እና የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን የተለያዩ የምርመራ ሪፖርቶች አቅርበዋል፡፡
የማህበረሰብ ልማት ፕሮግራም በሚል ስያሜ የዛሬ ሦስት ዓመት በጋምቤላ በተካሄደ የሰፈራ ፕሮግራም ከመኖሪያ መሬታቸው እንደተፈናቀሉ የገለፁት ገበሬው፤ ከመኖሪያዬ ልፈናቀል አይገባም በማለት ይዞታዬን ለመከላከል ስለጣርኩ አስከፊ ስቃይና እንግልት ደርሶብኛል ሲሉ ለለንደን ፍ/ቤት አቤቱታ አቅርበዋል፡፡ የአራት ልጆች አባት እንደሆኑ የገለፁት እኚሁ ገበሬ፤ ቤተሰቦቼን ችግር ላይ ጥዬ ወደ ኬንያ ለመሰደድና በመጠለያ ጣቢያ ለመኖር  ተገድጃለሁ ብለዋል፡፡ የእንግሊዝ መንግስት የሰብዓዊ መብት ጥሰት ለተፈፀመበት የሰፈራ ፕሮግራም የገንዘብ ድጋፍ በመስጠቱ ተጠያቂ  መሆን ይኖርበታል፤ ላደረሰብኝ በደልም ካሳ መክፈል አለበት ሲሉ ፍ/ቤቱን ጠይቀዋል - ኢትዮጵያዊው ገበሬ፡፡ የእንግሊዝ መንግስት ባለፉት አራት አመታት ከ1.3 ቢሊዮን ፓውንድ በላይ (አሁን ባለው የምንዛሬ መጠን ከ40 ቢሊዮን ብር በላይ) እርዳታ መስጠቱ የሚታወቅ ሲሆን፤ ዘንድሮም አለማቀፍ የልማት ድርጅት በተሰኘው መስሪያ ቤት አማካኝነት 10 ቢሊዮን ብር ገደማ እርዳታ እንደሚሰጥ ከሳምንት በፊት ገልጿል፡፡
እርዳታው ለሌላ ጉዳይ ሳይሆን፤ የጤና፣ የትምህርት፣ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ለመሳሰሉት የመሰረተ ልማት ማስፋፊያ ስራዎች የሚውል እንደሆነ የተናገሩት የእንግሊዝ መንግስት አለማቀፍ ልማት ድርጅት ቃል አቀባይ፤ ለሰፈራ ፕሮግራም የገንዘብ ድጋፍ አልሰጠንም ብለዋል፡፡
ከሰፈራ ፕሮግራሙ ጋር የእንግሊዝ መንግስት ግንኙነት እንደሌለው በመግለጽም፤ በኢትዮጵያዊው ገበሬ የቀረበው ክስ ውድቅ ሊደረግ ይገባል ብለዋል - የእንግሊዝ መንግስት ባለስልጣናት፡፡ የለንደኑ ከፍተኛ ፍ/ቤት ግን የቀረበለትን ክስ ውድቅ አላደረገም፡፡ ከሳሹ ገበሬ፣ “የእንግሊዝ መንግስት ለሰፈራ ፕሮግራም የገንዘብ ድጋፍ አድርጓል” ብለው የማመን መብት እንዳላቸው ፍ/ቤቱ ገልፆ፤ የክሱ ፍሬ ነገር በአግባቡ መመርመር አለበት በማለት ክሱን ለማየት ወስኗል፡፡  የሰፈራ ፕሮግራሙ ድህነትን ለመቀነስ ታስቦ በኢትዮጵያ መንግስት ተግባራዊ መደረጉን የገለጸው ቢቢሲ፤ ሂዩማን ራይትስ ዎች ከሁለት አመታት በፊት ባወጣው ሪፖርት፣ በጋምቤላ ክልል 70 ሺህ ያህል ዜጎች ያለፈቃዳቸው ከይዞታቸው ተነስተው በቂ ምግብ፣ የእርሻ ቦታና የመሰረተ ልማት አውታር ወደሌሉባቸው መንደሮች ተዛውረዋል ማለቱን አስታውሷል፡፡
የከሳሹ ገበሬ ስም ያልተጠቀሰው “የቤተሰቦቼ ደህንነት ያሰጋኛል” በማለታቸው እንደሆነ የገለፀው ዴይሊ ሜይል በበኩሉ፣ ገበሬው በጠበቆች አማካኝነት ክስ ለማቅረብና ለመከራከር በአስር ሺዎች ፓውንድ የሚገመት ገንዘብ እንደሚያስፈልጋቸውና ወጪው የሚሸፈነው በእንግሊዝ መንግስት እንደሆነ ጠቁሟል፡፡ ኢትዮጵያን ለመሳሰሉ አገራት በየአመቱ በሚመደበው እርዳታ ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚባክንና ሸክሙ በእንግሊዛዊያን ግብር ከፋዮች ትከሻ ላይ እንደሚያርፍ በመዘገብ የሚታወቀው ዴይሊ ሜይል፤ ኬንያ ውስጥ የሚኖር የሌላ አገር ዜጋ ክስ የሚመሰርተውና ካሳ የሚከፈለው በእንግሊዝ ግብር ከፋይ ዜጐች ኪሳራ ነው የሚል ተቃውሞ እንደተፈጠረ ገልጿል፡፡ ክስ አቅራቢው ገበሬ በበኩላቸው፤ በፍ/ቤቱ ውሳኔ ካሳ ከተከፈላቸው ገንዘቡን ለበጐ አድራጐት እንደሚያውሉት ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

ለማይክሮ ሶፍት መስራችና ባለቤት ለአሜሪካዊው ቢሊየነር ቢል ጌትስ በመጪው ሐሙስ  የክብር ዶክትሬት እንደሚሰጥ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ  አስታወቀ፡፡  ቢል ጌትስ የክብር ዶክትሬቱን ለመቀበል በሚቀጥለው ሳምንት ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመጡ ዩኒቨርሲቲው ማረጋገጡን ለአዲስ አድማስ ገልጿል።
ቢል ጌትስ የማይክሮሶፍት ኩባንያን በማቋቋም ባገኙት ሃብት አፍሪካውያን ተማሪዎችን የቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ማድረጋቸውና በቢል እና ሚሊንዳ ጌትስ ፋውንዴሽን አማካኝነት በኢትዮጵያ በተለያዩ የበጎ አድራጎት ስራዎች ላይ መሰማራታቸው ለክብር ዶክትሬቱ እንዳበቃቸው ተጠቁሟል፡፡
አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ባለፈው ቅዳሜ  8ሺህ ተማሪዎችን ያስመረቀ ሲሆን አትሌት ጥሩነሽ ዲባባን ጨምሮ ለ4 እውቅ ሰዎች የክብር ዶክትሬት ሰጥቷል። የቢል ጌትስ የክብር ዶክትሬት አሰጣጥ በተለየ ፕሮግራም እንዲካሄድ የተወሰነው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ስምምነት የተዘጋጀ በመሆኑ ነው ያለው ዩኒቨርሲቲው፤ በመንግስት ደረጃ የክብር ዶክትሬት ሲሰጥ የአሁኑ የመጀመሪያው እንደሆነ ገልጿል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ በኔልሰን ማንዴላ አዳራሽ በመጪው ሃሙስ  በሚከናወነው የክብር ዶክትሬት አሰጣጥ ልዩ ስነ ስርአት ላይ ጥሪ የተደረገላቸው የውጭ አገር እንግዶች፣ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት፣ የዩኒቨርሲቲው አመራሮችና ምሁራን እንደሚገኙ ታውቋል፡፡
የዓለማችን እውቁ ባለሃብት ቢል ጌትስ ላለፉት 10 ዓመታት በሃብቱ መጠን ከዓለም አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ይዞ ላይ በመሆን የቆየ ሲሆን ዘንድሮም በ79.1 ቢሊዮን ዶላር ሃብት በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ፎርብስ መጽሔት የወጣው መረጃ ይጠቁማል። ቢል ጌትስ አሁን በግዙፍነቱ የሚታወቀውን ማይክሮሶፍት ለመመስረት ትምህርቱን አቋርጦ ከወጣበት ሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ ጨምሮ ከተለያዩ የአለማችን ታላላቅ ዩኒቨርሲቲዎች ስምንት ያህል የክብር ዶክትሬቶችን እንዳገኘ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Published in ዜና

           ሰኔ 21 ቀን 2006 ዓ.ም በታተመው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ “ዕለት ደራሽ የዕርዳታ ትራንስፖርት ድርጅት ብዙ ሚሊዮን ብሮች በሙስና ተመዝብሯል ተባለ” በሚል ርዕስ የድርጅቱ የሕግ አገልግሎት ኃላፊ፣ የድርጅቱ የስነ-ምግባር መኮንን እና የመሰረታዊ ሰራተኛ ማህበር ም/ሊቀመንበር ለጋዜጣው ዝግጅት ክፍል አቀረቡ የተባለውን ጥቆማ በተመለከተ የሰራችሁትን ዘገባ ለንባብ ማብቃታችሁ ይታወሳል፡፡
ጋዜጣው ለሕዝብ የወገነና ለሁሉም በእኩል አገልጋይነት የቆመ ነው ብለን ስለምናምን ጠቋሚዎች ላቀረቡት ጥቆማ በማስረጃ የተደገፉ ምላሾች ለመስጠት እንወዳለን፡፡
በቅድሚያ ከጠቋሚዎች መሀከል በተለይም የሕግ አገልግሎት ኃላፊውና የስነ-ምግባር መኮንኑ የተሻሻለውን በፌደራል የስነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 433/1997 አንቀታ 27/7 የተገለፀውን ድንጋጌ በመጣስ፣ ጠቋሚዎች ለፌደራል የስነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ያቀረቡት ጥቆማ በምርመራ ላይ መሆኑን እያወቁ፣ ምርመራውን ከያዘው ክፍል ፈቃድ ውጪ ስለሁኔታው መጻፋቸው ለሕግ የበላይነት ያላቸውን አነስተኛ ግምት ያሳያል፡፡ ይህም ሊሆን አይችልም ከተባለ የጥቆማቸውን ውጤት ቀድመው በመገመት የመጨረሻውን የስም ማጥፋት ዘመቻ በማካሄድ የድርጅቱን ስም፣ ክብርና ዝና በማጉደፍ ከድርጅታችን ጋር ጥሩ የስራ ግንኙነት ያላቸውን መንግስታዊም ሆኑ የግል ድርጅቶች ጥርጣሬ ውስጥ እንዲገቡና ከድርጅቱ ጋር ቀጣይ ግንኙነት እንዳይኖራቸው በማድረግ ድርጅቱ ከዕድገት ጉዞው እንዲገታ ዛሬም ተኝተው እንደማያድሩ ያሳያል፡፡ ስለሆነም የድርጅቱ ማኔጅመንት ለሕግ ያለውን ክብርና ተገዥነት ግምት ውስጥ በማስገባት ለቀረቡት ጥቆማዎች ዘርዘር ያለ ምላሽ ከመስጠት ተቆጥቦ፣ ጠቋሚዎች ለጋዜጣው ባቀረቡዋቸው ጥቆማዎች ጠቅለል ያሉ ምላሾች ለመስጠት ተገዷል፡፡
ጠቋሚዎች በዚሁ ጋዜጣ እንደገለጹት ብዙ ሚሊዮን ብሮች በሙስና ተመዝብሯል በማለት ድርጅቱን በበላይት ለሚመራው የሥራ አመራር ቦርድ ያቀረቡ ሲሆን ቦርዱ በተቋቋመው ኮሚቴ ጥቆማው ተጣርቶ ውድቅ ሲሆንባቸው በቅርፅ ተመሳሳይነት ያላቸው በይዘት ተመሳሳይነት የሌላቸውን ጥቆማዎቻቸውን በፌደራል ስነ-ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽንና ሌሎች ጉዳዩ ይመለከታቸዋል ላሉዋቸው መንግስታዊ ተቋማት አቅርበዋል፡፡
ጠቋሚዎች በሙስና ተመዝብሯል ብለው በዝርዝር የገለጹዋቸው ነጥቦች፡-
ድርጅቱ የበላይ ተቆጣጣሪ መስሪያቤት ማለት በግብርና ሚኒስቴር የተቋቋመና ሦስት አካላት ያሉበት የባለሙያዎች ቡድን የማጣራት ስራ አከናውኖ ውጤቱን /ሪፖርቱን/ በፌደራል የስነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን አቅርቧል፤
በፌደራል የስነ-ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን የሙስና መከላከል ዳይሬክቶሬት ባለሙያዎችን መድቦ የድርጅቱን የግዥ አፈፃፀም ስርአት በተመለከተ የማጣራት ሥራ ተከናውኖ የምርመራው ሪፖርት ቅጂ ለድርጅቱ ደርሷል፡፡ ይሁን እንጂ በምርመራው ሪፖርት ጠቋሚዎቹ እንዳሉት፤ ድርጅቱ የግዥ መምሪያ የለውም፣ በተሟላ የግዥ እቅድ አይመራም፣ ወዘተ… በማለት ለአንባቢ በቂ ስእል በማይሰጥና ግራ በሚያጋባ መልኩ አልተገለፀም፡፡
ድርጅቱ አዲስ ሰራተኞችን የሚቀጥርበት ግልፅ የሆነ መመሪያና ደንብ ያለው በመሆኑ በህገወጥ መንገድ የተቀጠረ አንድም ሰራተኛ የለም፡፡ ድርጅቱ ያሉት ሁለት የመለዋወጫ እና አንድ የፅ/መሣሪያዎች መጋዘኖች ሲሆኑ ወደመጋዘኑ ለሚገቡም ሆነ ለሚወጡ መለዋወጫዎችና የጽሕፈት መሳሪዎች ተገቢው የገቢና የወጪ ሰነድ እየተዘጋጀላቸው አገልግሎት የሚሰጡ ናቸው፡፡ በመጋዘኖቹ ውስጥ የሚገኙ ንብረቶችን ትክክለኛነት ለማረጋገጥ አመታዊ የንብረት ቆጠራ በማካሄድ ከሒሳብ መዝገብ ጋር እንዲታረቅ ይደረጋል፡፡
የሂሳብ ማወራረጃ ደጋፊ ሰነዶች እንደወጪው አይነት የተለያዩ በመሆናቸው፣ የትኞቹ አይነት ደጋፊ ሰነዶች እንዲጠፉ፣ መቼ ስራ ላይ የዋሉና የየትኞቹ ተሽከርካሪዎች የተጠቀሙበት የጭነት ማዘዣዎችና የነዳጅ መጠየቂያ ፓዶች ሆን ብለው እንዲጠፉ እንደተደረገ የቀረበልን ማስረጃ የለም፡፡ እነዚህ ሰነዶች ደግሞ የሂሳብ ሰነዶች በመሆናቸው ድርጅቱ በየዓመቱ ሂሳቡን በወጪ ኦዲተሮች ሲያስመረምር በኦዲተሮች ልዩ ትኩረት ተሰጥቷቸው ምርመራ የሚደረግባቸው በመሆኑ በጠቋሚዎቹ እንደተገለፀው የሚሰወሩ አይደሉም፡፡
ድርጅቱ ያለጨረታ የገዛቸው የኢንጀክሽን ፓምፖች የሉም፡፡ ይሁን እንጂ የቺፕውድ ግዥና ከቆሙ የጭነት ተሸከርካሪዎች የተፈቱ አሮጌ መለዋወጫዎችን /ካኒባላይዜሽን/ በተመለከተ በፌደራል የስነ-ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽን በተመደቡ ኦዲተሮች ተገቢው ምርመራ ተከናውኖ የምርመራው ሪፖርቱ ቀርቧል፡፡ ውጤቱ እየተጠበቀ ይገኛል፡፡
የድርጅቱን የሂሳብ አያያዝ በተመለከተ በፌደራል የስነ-ምግባርና ጸረ-ሙስና  ኮሚሽን በተመደቡ የውጭ ኦዲተሮች ተገቢው ምርመራ ተከናውኖ የምርመራው ሪፖርቱ ለኮሚሽኑ ቀርቧል፡፡ ከቀረበው የኦዲት ሪፖርት ቅጅ መረዳት እንደተቻለው ብር 25 ሚሊዮን የመንግስት ገንዘብ ስለመመዝበሩ፣ የሂሳብ ማወራረጃ ደጋፊ ሰነዶች በመጥፋታቸው ደግሞ ከብር 5 ሚሊዮን በላይ ስለመመዝበሩ በምርመራው ሪፖርት የተገለፀ ነገር የለም፡፡ ከምርመራው ሪፖርት ውጪ ተመዘበረ ተብሎ የተገለፀው ገንዘብ ጠቋሚዎች አእምሮ ውስጥ ብቻ የተፃፈ ወይም የተሳለ ስእል ነው ብለን እንገምታለን፡፡ ጠቋሚዎች እንዳሉት፤ በሂሳብ ምርመራ ወቅት በጉድለት የተመዘገበ ገንዘብ ተመርማሪው በፈለገበት ጊዜ የጎደለው ብር ተገኝቷል ብሎ ምርመራውን ላከናወነው የኦዲት ቡድን (ኦዲተር) ምለፁ ብቻ ያድነዋል ብሎ ማሰብ ጠቋሚዎች ስለኦዲት ሥራ ያለማወቃቸውን የማያውቁ መሆናቸውን የሚገልፅ ወይም እራሳቸውን እንደአዋቂ በመቁጠር ከሙያው ባለቤቶች ጠይቆ ለመረዳት ካለመፈለግ የመነጨ መሆኑ ልብ ሊባል ይገባዋል፡፡
በአጠቃላይ ደርጅቱ ከ1997-2001 ዓ.ም በነበሩት 5 ዓመታት በኪሳራ ሲጓዝ የነበረና ለሰራተኛው ደመወዝ እንኳ ለመክፈል አቅቶት ለመውደቅ ሲንገዳገድ የነበረ መሆኑን የድርጅቱን ትክክለኛ ገፅታ ከሚያሳየውና በውጪ ኦዲተሮች ትክክለኛነቱ የተረጋገጠውን የሂሳብ መግለጫዎች ማየት ይቻላል፡፡
ይሁን እንጂ ይህ በጠቋሚዎች የስም ማጥፋት ዘመቻ እየተካሄደበት የሚገኘው ማኔጅመንት፤ ከተቋቋመበት ከ2002-2005 ዓ.ም ድርጅቱ ይጓዝ ከነበረበት የቁልቁለት መንገድ በማውጣት፣ በውጪ ኦዲተሮች የተረጋገጠ ትርፍ በማስመዝገብና የአገልግሎት ዘመናቸውን የጨረሱ የጭነት ተሽከርካሪዎች በአዲስ ለመተካት በተደረገ ጥረት 400 ኩንታል የመጫን አቅም ያላቸው 15 ዘመናዊ የጭነት ተሽከርካሪዎች ባለቤት እንዲሆን ያደረገ ሲሆን ዛሬም መንግስት በሰጠው ምቹ ዕድል ከ560 ኩንታል በላይ የመጫን አቅም ያላቸው 20 የጭነት ተሽከርካሪዎች ባለቤት እንዲሆን በማድረግ ላይ የሚገኝና የድርጅቱ ሰራተኞች ከ2002 ዓ.ም በፊት አግኝተውት የማያውቁትን ከ2-3 ወር ደመወዝ ማበረታቻ /ቦነስ/ በየዓመቱ እንዲያገኙ ያደረገ ነው፡፡ ይህ ሊዋጥላቸው ያልቻሉ ከማስረጃ ይልቅ ለአሉባልታ ቅርብ የሆኑ፣ የማኔጅመንቱን ጥንካሬና ከስራ አመራር ቦርድ ጋር ያለው የጠበቀ የስራ ግንኙነት ያላስደሰታቸው ጠቋሚዎች በሚያናፍሱት ተጨባጭ ያልሆነ ክስ ተደናግጦ ማኔጅመንቱ ድርጅቱን ለማሳደግ እያደረገ ያለውን ጥረት አይገታም፡፡
እነዚህ ግለሰቦች በድርጊታቸው በሰራተኛው የተተፉበት ወቅት ላይ ስለሚገኙ በማስረጃ ባልተደገፉ ጥቆማቸው ድርጅቱ በአዲስ መልክ እየተደራጀ ባለበት በዚህ ወቅት በመሯሯጥ በመገናኛ ብዙሀን የድርጅቱን ስምና ክብር በማጉደፍ የስልጣን ጥማቸውን /ፍላጎታቸውን/ ለማርካት ያላቸውን ፍላጎት ለማሳካት የማያንኳኩት የባለስልጣን በር፣ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም፡፡
ከጠቋሚዎቹ መሃል ህይወታችን ለአደጋ ተጋልጧል፣ ሁለት ጊዜ በጥይት ተስቻለሁ የሚሉት የቀድሞው የደርግ ሻምበልና የአሁኑ አቶ ያለው አክሊሉ የፈጠራ ወሬዎችን ሲያወሩና ሲያስወሩ ድፍን አንድ አመት ሞልቷቸዋል፡፡ የነፍስ ግድያ ሙከራ ተደረገብኝ ለሚሉት የሀሰት አሉባልታቸው ይረዳቸው ዘንድ እነሱ ባሰቡትና በፈለጉት መልኩ የማኔጅመንት አባላት ላይ የትንኮሳ ስራ እየሰሩ ያሉ ቢሆንም የማኔጅመንት አባላቱ ጉዳዩ በፍ/ቤት እንዲታይላቸው ከማድረግ ባለፈ ጠቋሚዎች ድርጅቱ ግቢ ውስጥ ብቻቸውን ውለው ቢያድሩ እንኳ ነብሳቸውን እስከማጥፋት የሚያደርስ ወንጀል ለመስራት ፍላጎት ያለው የማኔጅመንት አባል እንደሌለ ልቦናቸው እያወቀ፣ ከድርጅቱ ውጪ ባሉ ወገኖች ከንቱ ውዳሴና ተቀባይነት ለማግኘት የሚያደርጉት የፕሮፓጋንዳ ዘመቻቸው አካል ነው፡፡
(ከ“ዕለት ደራሽ የእርዳታ
ትራንስፖርት ድርጅት” ማኔጅመንት)

Published in ዜና
Saturday, 12 July 2014 12:55

አውሮፓ 10 ደቡብ አሜሪካ 9

20ኛው የዓለም ዋንጫ ዛሬ እና ነገ በሚደረጉት ሁለት የደረጃ እና የዋንጫ ጨዋታዎች ያበቃል፡፡ ዛሬ በደረጃ ጨዋታ አዘጋጇ አገር ብራዚል ከሆላንድ የሚጫወቱ ሲሆን በነገው እለት ደግሞ በዋንጫ ጨዋታ አውሮፓን የምትወክለው ጀርመንና ከደቡብ አሜሪካ የተወከለችው አርጀንቲና ይገናኛሉ፡፡ ጀርመንና አርጀንቲና በዓለም ዋንጫ ፍፃሜ ጨዋታ ለሶስተኛ ግዜ መገናኘታቸው ነው፡፡
በዓለም ዋንጫ የፍፃሜ ጨዋታ ለስምንተኛ ጊዜ የሚሰለፈው የጀርመን ብሄራዊ ቡድን  ለ4ኛ ጊዜ የውድድሩ ሻምፒዮን በመሆን በዓለም ዋንጫ ድል ብዛት ሁለተኛ ደረጃ ከያዘችው ጣሊያን ጋር ክብረወሰኑን ለመጋራት ያነጣጥራል፡፡ አርጀንቲና ደግሞ ሶስተኛ የሻምፒዮናነት ክብሯን በማሳካት የጀርመንን የውጤት ክብረወሰን ለመስተካከል ታቅዳለች፡፡ በሌላ በኩል የሁለቱ ቡድኖች ውጤታማነት በአውሮፓ እና በደቡብ አሜሪካ አህጉራት መካከል ያለውን የዋንጫ ፉክክር የሚወስን ነው፡፡
ከ20ኛው ዓለም ዋንጫ በፊት በሻምፒዮናነት ክብር አውሮፓ 10ለ9 ደቡብ አሜሪካን ይመራል፡፡


ጀርመን
ብሄራዊ 11 ወይም ‹ዘ ማንሻፍትስ› በሚል መጠርያ የሚታወቀው የጀርመን ብሄራዊ ቡድን ሌሎች ተጨማሪ ቅፅል ስሞች በሰንደቅ አለማ እና ማልያ ቀለማት እና ምልክቶች ንስሮች እና ጥቁርና ነጭ ተብሎም ይታወቃል፡፡
ለብሄራዊ ቡድኑ ብዙ የተሰለፈ - ሉተር ማትያስ 150 ጨዋታዎች
ለብሄራዊ ቡድኑ ብዙ ያገባ -ሚሮስላቭ ክሎሰ 71 ጎሎች
የፊፋ ደረጃ -2
የመጀመሪያ ኢንተርናሽናል ጨዋታ - ከ106 ዓመት በፊት
የዓለም ዋንጫ ተሳትፎ እና ውጤት 18 ጊዜ - 3 ጊዜ ሻምፒዮን (1954፤ 1974ና 1990 እኤአ)
ከ20ኛው ዓለም ዋንጫ  የፍፃሜ ጨዋታ በፊት በዓለም ዋንጫ 105 ጨዋታዎች- 65 ድል- 20 አቻ- 20 ሽንፈት - 223 አገባ 121 ገባበት
የአውሮፓ ዋንጫ ተሳትፎ እና ውጤት 11 ጊዜ -3 ጊዜ ሻምፒዮን (1972፤ 1980ና 1996 እኤአ)
ጀርመን እግር ኳሷን እዚህ ለማድረስ ከ2000 እ.ኤ.አ ጀምሮ አገር አቀፍ የዕድገት ፕሮግራም በመንደፍ ስትሰራ ቆይታለች፡፡ ከዚህ የለውጥ እንቅስቃሴ በፊት የጀርመን ብሄራዊ ቡድን በዓለም እና በአውሮፓ ዋንጫ ተሳትፎዎቹ ከምድብ ማጣሪያ ማለፍ ሲያዳግተው ነበር፡፡ በጀርመን እግር ኳስ ፌደሬሽን እና በአገሪቱ ከፍተኛ የስፖርት ባለሙያዎች እና አሰልጣኞች ተግባራዊ የሆነው ፕሮግራም ከ20 ሺ በላይ የስፖርት መምህሮችና ባለሙያዎች በማሳተፍ በጀርመን 366 ክልሎች ታዳጊ ተጨዋቾች በመመልመልና በማሰልጠን ተሰርቶበታል፡፡  ከአሰልጣኞች መካከል አሁን የአሜሪካ ብሄራዊ ቡድንን የሚያሰለጥነው እና ቀድሞ የጀርመን ዋና አሰልጣኝ የነበረው ጀርገን ክሊንስማንና የአሁኑ ዋና አሰልጣኝ ጆኦኪም ሎው ዋና በዚህ ፕሮግራም ተዋናዮች ነበሩ፡፡


አርጀንቲና
‹ላ አልባሴላስቴ› በሚል ቅፅል ስሙ የሚጠራው የአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድን በሰንደቅ አለማ ቀለም እና በማልያዎቹ ቀለማት ነጭና ውሃ ሰማያዊ  ይባላል፡፡
ለብሄራዊ ቡድኑ ብዙ የተሰለፈ - ሃቪዬር ዛኔቲ 145 ጨዋታዎች
ለብሄራዊ ቡድኑ ብዙ ያገባ -ጋብሬል ባቲስቱታ 56 ጎሎች
የፊፋ ደረጃ -5
የመጀመሪያ ኢንተርናሽናል ጨዋታ - ከ113 ዓመት በፊት
የዓለም ዋንጫ ተሳትፎ እና ውጤት 15 ጊዜ - 2 ጊዜ ሻምፒዮን (1978ና 1986 እኤአ)
ከ20ኛው ዓለም ዋንጫ  የፍፃሜ ጨዋታ በፊት በዓለም ዋንጫ 75 ጨዋታዎች -41 ድል -13 አቻ -20 ሽንፈት - 131 አገባ 83 ገባበት
የኮፓ አሜሪካ ተሳትፎ እና ውጤት 39 ጊዜ -14 ጊዜ ሻምፒዮን
ካለፉት 3 ዓመታት ወዲህ  በዓለም የእግር ኳስ ገበያ ከፍተኛ ብዛት ያላቸውን ፕሮፌሽናል ተጨዋቾች በማቅረብ አርጀንቲና አንደኛ ደረጃ ተሰጥቷታል፡፡ በመላው አለም በሚካሄዱ የሊግ ውድድሮች ላይ ተሳታፊ በሆኑ ክለቦች ከ1700  በላይ አርጀንቲናውያን ፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ይገኛሉ፡፡ ብራዚላውያን ፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ብዛታቸው 1400 ነው፡፡

    ጀርመንና አርጀንቲና በዓለም ዋንጫ 5 የሻምፕዮናነት ክብሮች  አግኝተዋል፡፡ ነገ በዓለም ዋንጫ የፍፃሜ ጨዋታ የሚገናኙት በታሪክ ለሶስተኛ ጊዜ ይሆናል፡፡  በሁለቱ የዓለም ዋንጫ ጨዋታዎች በ1986 እኤአ ላይ አርንጀቲና ስታሽንፍ በ1990 እኤአ ደግሞ ጀርመን አሸንፋለች፡፡ ከ20ኛው የዓለም ዋንጫ የፍፃሜ ፍልሚያ በፊት የአውሮፓዋ ጀርመን ለ3 ጊዜያት (በ1954፤ በ1974 እና በ1990 እኤአ) እንዲሁም አርጀንቲና ለ2 ጊዜያት (በ1978 እና በ1986 እኤአ) የዓለም ሻምፒዮን ሆነዋል፡፡ የእነዚህ የዓለም ዋንጫ ድሎች ታሪክ ከዚህ በታች የቀረበው ነው፡፡
በፊፋ የወርቅ ኢዮቤልዩ የደመቀው የጀርመን የመጀመርያ ድል
በ1954 እ.ኤ.አ 5ኛው ዓለም ዋንጫ  በአውሮፓዊቷ አገር ስዊዘርላንድ የተካሄደ ነበር፡፡   ሁለተኛው ዓለም ጦርነት ትኩሳት ከረገበ ከ8 ዓመታት በኋላ ነው፡፡ ይህ ዓለም ዋንጫ ከዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ፊፋ 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ ክብረ በዓል ጋር መያያዙ ልዩ ያደርገዋል፡፡ የዓለም ዋንጫ የቴሌቨዥን ስርጭት በጥቁርና ነጭ ለመጀመርያ ጊዜ የተከናወነበትም ነበር፡፡ በሌላ በኩል  በአጠቃላይ 140 ጐሎች ከመረብ ማረፋቸውና ባንድ ጨዋታ በአማካይ 5.38 ጐሎች መመዝገቡ እስካሁን በሪከርድነት ቆይቷል፡፡ በ5ኛው የዓለም ዋንጫ ፍፃሜ ጨዋታ ላይ የተገናኙት ምዕራብ ጀርመንና ሃንጋሪ ነበሩ፡፡ የጀርመን ብሄራዊ ቡድን በካፒታሊዝም ስርዓት ይተዳደር በነበረው የአገሪቱ ክፍል ተወካይነት ምእራብ ጀርመን ተብሎ የተሳተፈ ነበር፡፡   በ1950ዎቹ ምርጥ ከሚባሉ  ቡድኖች አንዱ የነበረውና እነ ፈረንስ ፑሽካሽ፣ ቦዝስክ ኮሲስኮና ሀይ ድግኡቲ የሚገኙበት የሃንጋሪ ብሄራዊ ቡድን ደግሞ የውድድሩ አስደናቂ አቋም ያሳየ ነበር፡፡ የፍፃሜው ፍልሚያ በስዊዘርላንዷ በርን ከተማ በሚገኘው የዋንክድሮፍ ስታድዮም ሲካሄድ ከ60ሺ በላይ ተመልካች ነበረው፡፡ የሃንጋሪ  ቡድን 2ለ0 ሲመራ ቢቆይም ከኋላ ተነስቶ 3 ጐሎችን በማስቆጠር 3ለ2 በሆነ ውጤት የምዕራብ ጀርመን  ብሄራዊ ቡድን አሸነፈ፡፡ ስለሆነም የመጀመሪያው የሻምፒዮንነት ክብር በማግኘት  የጁሌዬስ ሪሜት ዋንጫን ተቀዳጅቷል፡፡ የምእራብ ጀርመን ደጋፊዎች ብሄራዊ ቡድናቸው የጁሌዬስ ሪሜት ዋንጫን ሲረከብ በስታድዬሙ ምእራብና ምስራቅ ጀርመንን የሚያዋህደውን መዝሙር እንዳሰሙ ታሪክ ያስታውሳል፡፡
የአሁኗ ዓለም ዋንጫ ለሽልማት ቀርባ ለአስተናጋጇ ጀርመን  ሁለተኛ ድል
10ኛውን የዓለም ዋንጫ  በ1974 እ.ኤ.አ  ላይ የተካሄደው በምዕራብ ጀርመን ነበር፡፡  በ9 ዓለም ዋንጫዎች ለሻምፒዮኑ አገር ስትሸለም የቆየችው የጁሌስ ሪሜት ዋንጫ በአዲስ ተቀይራ የቀረበችበት ዓለም ዋንጫ ነበር፡፡ የጁሊዬስ ሪሜት ዋንጫን  ብራዚል ለሶስተኛ ጊዜ ወስዳ በማስቀረቷ  አዲሷ የፊፋ ዓለም ዋንጫ መሰራቷ አስፈላጊ ሆኗል፡፡ አዲስ የዋንጫ  ሽልማት ከ7 የተለያዩ አገሮች ቀራፂዎች የሰሯቸው 53 የተለያዩ ዲዛይኖች ለውድድር ቀረቡ፡፡ በጣሊያናዊው ቀራፂ ሲልቪዮ ጋዚንጋ  የቀረበችው ዋንጫ ተመረጠች፡፡ 10ኛው ዓለም ዋንጫ ከቀዳሚዎቹ 9 ዓለም ዋንጫዎች ልዩ ካደረጉት ሁኔታዎች አንዱ በባለቀለም ቴሌቪዥን ስርጭት ማግኘቱ ነበር፡፡ በሌላ በኩል የሆላንዳዊያን የ‹ቶታል ፉትቦል› የአጨዋወት ፍልስፍና የሚወሳ ታሪክ ነበር፡፡ በዋንጫው ጨዋታ የምዕራብ ጀርመን ብሔራዊ ቡድን እና በቶታል ፉትቦል የተደነቀው የሆላንድ ብሄራዊ ቡድን ተገናኙ፡፡ ምዕራብ ጀርመን  በብሄራዊ ቡድኑ አምበል  ፍራንዝ ቤከንባወር  እና  በዋና አሰልጣኝ ሄልሙት ሾን  የተመራ ነበር፡፡ ሆላንድ ደግሞ በአሰልጣኝ ሩኒስ ሚሸልስና በታዋቂው ተጨዋች ዮሃን ክሮይፍ አስደናቂ አቋም በማሳየት ለዋንጫው የታጨ ነበር፡፡  የምዕራብ ጀርመን ብሔራዊ ቡድን 2ለ1 በማሸነፍ አዲሷን የዓለም ዋንጫ ለመጀመርያ ጊዜ እንዲሁም በውድድሩ ታሪክ ሁለተኛው የዓለም ሻምፒዮናነት ክብር አስመዘገበ፡፡ ለምዕራብ ጀርመን የማሸነፊያዋን ግብ ያስቆጠረው ዘ ቦምበር በሚል ቅል ስሙ የሚታወቀው ገርድ ሙለር ነበር፡፡ ጀርመናዊያን ቄሳሩ እያሉ በሚያሞግሱት ፍራንዝ ቤከንባወር የተመራው ብሔራዊ ቡድኑ ውስጥ ሚዬርና በርቲ ቮጎትስ የተባሉ ምርጥ ተጨዋቾች ይታወሳሉ፡፡
የአርጀንቲና የመጀመርያ ድል
በ1978 እ.ኤ.አ 11ኛውን  የዓለም ዋንጫ የማስተናገድ እድል ያገኘችው አርጀንቲና ናት፡፡ በ1ኛው ዓለም ዋንጫ ለፍፃሜ ተጫውታ ዋንጫውን በኡራጋይ ከተነጠቀች ከ48 ዓመታት በኋላ ወደ እግር ኳስ ሃያልነቷ ለመመለስ የበቃችበት ነበር፡፡  በዓለም ዋንጫው ዋዜማ አርጀንቲናን ያስተዳድር የነበረው መንግስት በመፈንቅለ መንግስት  ተገልብጦ አምባገነኑ መሪ ጄኔራል ቪዴላ ስልጣን መያዛቸው ነበር፡፡ ስለሆነም የዓለም ዋንጫው መሰናዶ በጄኔራል ቪዴላ መንግስት በሰብአዊ መብት ጥሰትና በአምባገነናዊ ስርአቱ ከበርካታ አገራት ተቃውሞ የተሰነዘርበት ነበር፡፡ የሻምፒዮናነት ክብሩን ለመጀመርያ ጊዜ ለማግኘት ተስፋ በማድረግ በ11ኛው የዓለም ዋንጫ ለፍፃሜ ጨዋታ የቀረቡት አስተናጋጇ አርጀንቲና እና ሆላንድ  ነበሩ፡፡ የፈረንሳዩ ለኢክዊፔ ጋዜጣ እና ሌሎች አለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃናት አስቀድመው ከተደረጉት 10 የዓለም ዋንጫዎች ምርጡ የፍፃሜ ፍልሚያ ተብሎ ነበር፡፡ አርጀንቲና 3ለ1 በሆነ ውጤት ሆላንድን በማሸነፍ  በታሪኳ ለመጀመርያ ጊዜ የዓለም ዋንጫ ድል አግኝታለች፡፡ በወቅቱ የአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድንን በዋና አሰልጣኝነት የመሩት ሴዛር ሜኖቲ ከቡድናቸው የ17 ዓመቱን ዲያጎ አርማንዶ ማራዶና መቀነሳቸው ቢያስተቻቸውም ቡድናቸው የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን ተከትሎት በነበረው ውበትን የተላበሰ አጨዋወት  አድናቆት አትርፈውበታል፡፡ ከተጨዋቾች አምበል የነበረው ዳንኤል ፓሳሬላ እና ማርዮ ኬምፐስ የተባለው አጥቂ ከፍተኛ አድናቆት ያተረፉ  ነበሩ፡፡ የውድድሩ ኮከብ ግብ አግቢ ሆኖ የጨረሰው ማርዮ ኬምፕስ በአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድን ከነበሩ  ተጨዋቾች መካከል  በፕሮፌሽናልነት በስፔን ላሊጋ ለሚወዳደረው ሻሌንሺያ ክለብ በመጫወት ብቸኛው ነበር፡፡
በማራዶና ጀብድ የአርጀንቲና ሁለተኛ ድል
13ኛው የዓለም ዋንጫ በ1986 እ.ኤ.አ ላይ በሰሜንና መካከለኛው አሜሪካ ዞን የምትገኘው ሜክሲኮ ጊዜ ያስተናገደችው ነበር፡፡  ይህ ዓለም ዋንጫ በመስተንግዶ ማራኪነት፤ በስታድዬሞች በታየው ሜክሲኳውያን ማዕበል የተባለው ድጋፍ አሰጣጥና በአርጀንቲናዊው ኮከብ ዲያጎ አርማንዶ ማራዶና ባሳየው የላቀ ችሎታ የማይረሳ  ነው፡፡  በዚህ ዓለም ዋንጫ ላይ በፍፃሜ ጨዋታ የተገናኙት አርጀንቲና ከምእራብ ጀርመን ጋር ነበር፡፡ ከ115ሺ በላይ ተመልካች ባስተናገደው ታላቁ አዝቴካ ስታድዬም የሁለቱ ቡድኖች ፍልሚያ 2ለ2 በሆነ ውጤት እስከ 83ኛው ደቂቃ ቆየ፡፡  ማራዶና ለቡድን አጋሩ ጆርጌ ቡርቻጋ አመቻችቶ ያቀበለው ምርጥ ኳስ አማካኝነት  የማሸነፊያ ጎል ተመዘገበችና በአርጀንቲና 3ለ2 አሸናፊነት ተጠናቀቀ፡፡ ከ30 ሚሊዮን በላይ አርጀንቲናውያንም በድሉ ፌሽታ መላው አገራቸውን በደስታ አጠልቅልቀው ደስታቸውን ገልፀዋል፡፡ አርጀንቲናን በአምበልነት እየመራ ለታላቁ የዓለም ዋንጫ ድል የበቃው ማራዶና  በአንድ ተጨዋች ጀብደኛነት ውድድረን ማሸነፍ እንደሚቻል ያሳየበት ነበር፡፡ አርጀንቲና እስከዋንጫው ባደረገችው ግስጋሴ ዲያጎ አርማንዶ ማራዶና አምስት ጎሎችን ከማግባቱም በላይ ለሌሎች  አምስት ግቦች መመዝገብ ምክንያትም ሆኗል፡፡ ማራዶና በምርጥ ችሎታው ዓለምን ማንበርከክ ቢችልም በተለይ በእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን ላይ በእጁ ያስቆጠራት ግብ ግን የብዙዎችን አድናቆት ወደ ቁጣ ቀይራዋለች፡፡ በወቅቱ ለንባብ የበቃው የፈረንሳዩ ጋዜጣ ሌኢክዌፔ ማራዶናን ‹‹ግማሽ መልዓክ ግማሽ ሰይጣን››  ብሎታል፡፡
የዓለም ዋንጫ ድል ሃትሪክ በጀርመን  
14ኛው ዓለም ዋንጫ በ1990 እኤአ ላይ በጣሊያን አዘጋጅነት የተደረገ ነው፡፡ በውድድሩ ታሪክ  ዝቅተኛ የግብ ብዛት የተመዘገበበት ወቅት ነበር፡፡ አዘጋጇ ጣሊያን በግማሽ ፍፃሜው ከጨዋታ ውጪ የሆነችው በአርጀንቲና ተሸንፋ ነበር፡፡ ዲያጎ አርማንዶ ማራዶና በአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድን ስለነበር ግን በክለብ ደረጃ የሚጫወትበት ናፖሊ ክለብ ደጋፊዎች ግራ ተጋብተው ነበር፡፡ ጣልያን ትተው እሱን እንደግፍ በሚል ተወዛግበዋል፡፡
በዚህ ዓለም ዋንጫ በፍፃሜ ጨዋታ የተገናኙት  በታሪክ ለሁለተኛ ጊዜ አርጀንቲና እና ምዕራብ ጀርመን ነበሩ፡፡ በሮም ኦሎምፒክ ስታድዬም በተደረገው ጨዋታ የምእራብ ጀርመን ብሔራዊ ቡድን  አርጀንቲናን 1ለ0 ረታ፡፡ ከአራት ዓመት በፊት በፍፃሜ ጨዋታ በታላቁ አዝቴካ ስታድዬም በማራዶና በተመራችው አርጀንቲና የደረሰበትን ሽንፈት በመበቀል ለ3ኛ ጊዜ የዓለም ሻምፒዮን መሆን ችሏል፡፡ በወቅቱ የቡድኑ አሰልጣኝ የነበረው ፍራንዝ ቤከን ባወር ደግሞ የዓለም ዋንጫን በተጨዋችነት በ1974 እኤአ ላይ ካሸነፈ ከ16 ዓመታት በኋላ በአሰልጣኝነት በማሸነፍ በውድድሩ ታሪክ አስደናቂ ክብረወሰን አስመዝግቧል፡፡

      ባለፉት 5 ዓለም ዋንጫዎ ኮከብ ግብ አግቢ ች ለግማሽ ፍፃሜ ከደረሰ 4 ቡድኖች ተገኝቷል፡፡ ግማሽ ፍፃሜ መግባት 7 ጨዋታ ማድረግ በመሆኑ ለፉክክር ያለውን እድል ያሰፋዋል፡፡ በኮከብ ግብ አግቢነት ፉክክር የኮሎምቢያው ጀምስ ሮድሪጌዝ በ6 ጎሎች እየመራ ነው፡፡ የጀርመኑ ቶማስ ሙለር በ5 ጎሎች የሚከተለው ሲሆን ሊዮኔል ሜሲ እና ኔይማር ዳሲልቫ በ4 ጎሎች ሶስተኛ ደረጃ አላቸው፡፡ ቶማስ ሙለር እና ሊዮኔል ሜሲ በዋንጫው ጨዋታ ከ1 በላይ ካገቡ ለወርቅ ጫማው ሽልማት እድል የሚኖራቸው ሲሆን እያንዳንዳቸው እኩል 3 ጎል ያስመዘገቡት የሆላንዶቹ ሮበን እና ቫንፕርሲ በደረጃ ጨዋታ ከሃትሪክ በላይ ጎል ካስመዘገቡም ሊያሸንፉ ይችላሉ፡፡ የጀርመኑ ቶማስ ሙለር በዋንጫ ጨዋታ አንድ ግብ በማስቆጠር በሁለት ተከታታይ ዓለም ዋንጫዎች በኮከብ ግብ አግቢነት በመጨረስ የወርቅ ጫማ ለመሸለም እድል የሚኖረው 3 ለጎል የበቁ ኳሶችን በማቀበል ነው፡፡ በኮከብ ተጨዋችነት የወርቅ ኳስ ተፎካካሪዎች የሆኑት የኮሎምቢያው ጀምስ ሮድሪጌዝ፤ የጀርመኑ ቶማስ ሙለር እና የአርጀንቲናው ሊዮኔል ሜሲ ናቸው፡፡ 

የኮሎምቢያው ጀምስ በ5 ጨዋታ 6 ጐል በማግባት  በ3 ግጥሚያዎች የጨዋታው ኮከብ ሽልማቶችን በመውሰድ እና ተጨማሪ ለጎል የበቁ ሁለት ኳሶችን በማቀበል ፉክክሩን እየመራ ነው፡፡ በዓለም ዋንጫው በ4 ግጥሚያዎች የጨዋታው ኮከብ ሆኖ የተመረጠው ሊዮኔል ሜሲ በዋንጫ ጨዋታ በሚኖረው ብቃት በኮከብ ተጨዋችነት የወርቅ ኳስ ለመሸለም ሰፊ እድል ይዟል፡፡ በዓለም ዋንጫው ኮከብ በረኛነት የወርቅ ጓንት ለመሸለም ሶስት በረኞች ዋና ተፎካካሪዎች ናቸው፡፡  የአርጀንቲናው ሰርጂዬ ሮሜሮ በ4 ጨዋታዎች ጐል አልገባበትም፡፡ የጀርመኑ ማኒዌል ኑዌር  ደግሞ በ3 ጨዋታ ጎል ያልተቆጠረበት ሲሆን በፍፃሜው የሚኖረው ብቃት ለመሸለም ሰፊ እድል አለው፡፡ በሶስት ግጥሚያዎች የጨዋታው ኮከብ ለመሆን የበቃው የኮስታሪካው ግብ ጠባቂ ኪዬሎር ናቫስ ሌላው ተፎካካሪ ነው፡፡

የውጤት ደረጃ ከ5 እስከ 32
በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ዛሬ እና ነገ በሚደረጉት ሁለት የደረጃ እና የዋንጫ ጨዋታዎች ላይ የሚሳተፉት አራቱ ቡድኖች ብራዚል፤ ሆላንድ፤ ጀርመንና አርጀንቲና በአጠቃላይ ውጤት ከ1 እስከ 4 የሚኖራቸውን ደረጃ ይወስናሉ፡፡  እስከ ሩብ ፍፃሜ ለመሳተፍ የበቁት 28 ቡድኖች ደግሞ ከ5ኛ ደረጃ ጀምሮ እስከ 28ኛ በቅደም ተከተል በውጤታቸው ደረጃ ተሰጥቷቸዋል፡፡ ለሩብ ፍፃሜ የበቁት እና እያንዳንዳቸው 14 ሚሊዮን ዶላር የሽልማት ገንዘብ የሚከፈላቸው 4 ብሄራዊ ቡድኖች ኮሎምቢያ፤ ቤልጅዬም ፈረንሳይና ኮስታሪካ  ከ5 እስከ 8ኛ ደረጃ ያገኛሉ፡፡ 16 ቡድኖች ለደረሱበት ጥሎ ማለፍ የበቁት እና እያንዳንዳቸው 9 ሚሊዮን ዶላር የሽልማት ገንዘብ የሚከፈላቸው 8 ብሄራዊ ቡድኖች ቺሊ፤  ሜክሲኮ፤ ስዊዘርላንድ፤ ኡራጋይ፤ ግሪክ፤ አልጄርያ፤ አሜሪካ እና ናይጄርያ ከ9 እስከ 16ኛ ደረጃ ያገኛሉ፡፡ በምድብ ማጣርያ ተሳትፏቸው የተወሰኑት እና እያንዳንዳቸው 8 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ሽልማት የሚከፈላቸው 16 ብሄራዊ ቡድኖች ኢኳዶር፤ ፖርቱጋል፤ ክሮሽያ፤ ቦስኒያ፤ አይቬሪኮስት፤ ጣሊያን፤ ስፔን፤ ራሽያ፤ ጋና፤ እንግሊዝ ደቡብ ኮርያ፤ ኢራን፤ ጃፓን፤ አውስትራሊያ፤ ሆንዱራስ እና ካሜሮን ከ17 እስከ 32ኛ ደረጃ ተሰጥቷቸዋል፡፡

ከስፖንሰሮች የተሳካለት አዲዳስ ነው
በ20ኛው ዓለም ዋንጫ  በከፍተኛ ደረጃ የማስተዋወቅ እና የማሻሻጥ ዘመቻ ካደረጉት ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ስኬታማ የሆነው የጀርመኑ የስፖርት ትጥቅ አምራች ኩባንያ አዲዳስ ነው፡፡ ፊፋ በዓለም ዋንጫው በአጋርነት ከሰሩት 8 ስፖንሰሮች 1.53 ቢሊዮን ዶላር አግኝቷል፡፡
አዲዳስ ከ20ኛው ዓለም ዋንጫ በተያያዘ ለማስተዋቂያ እና ለገበያ ማስፋት ዘመቻው ወጭ ያደረገው 85 ሚሊዮን ዶላር ሲሆን በውድድሩ ያቀረባት ብራዙካ የተባለች ኳስ ባተረፈችው ተወዳጅነት እንዲሁም ታኬታና ማልያ ያቀረበላቸው 9 ብሄራዊ ቡድኖች በተለይ ጀርመን ባስመዘገቡት ስኬት እስከ  2.7 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ይጠብቃል፡፡ በዚህ ገቢም በዓለም ዋንጫው ስኬታማ በመሆን የጀርመኑ አዲዳስ ግንባር ቀደም ይሆናል፡፡
የቅርብ ተቀናቃኙ የሆነው የአሜሪካው የስፖርት ትጥቅ አምራች ኩባንያ በዓለም ዋንጫው የማስተዋወቅ እና የማሻሻጥ ዘመቻው  70 ሚሊዮን ዶላር ወጭ አድርጎ  እስከ 1.9 ቢሊዮን ዶላር ገቢ በመጠበቅ ይከተላል፡፡ ለናይኪ ገበያ መቀነስ የማልያ እና የትጥቅ ስፖንሰር ከሆነለቻቸው አስር ብሄራዊ ቡድኖች በተለይ አዘጋጇ ብራዚል ለዋንጫ አለመድረሷ ነው፡፡ ከሌሎች የዓለም ዋንጫ ስፖንሰሮች ለማስተዋወቅ እና ለማሻሻጥ ዘመቻው ኮካ ኮላ በብራዚል ብቻ 600 ሚሊዮን ዶላር ወጭ ማድረጉ ከፍተኛው ሆኖ ይጠቀሳል፡፡

የማህጸን ኪራይ ማለት ምን ማለት ነው?
ለእነማን ነው የሚሰራው?
ማህጸንን የሚያከራዩ ሴቶች በምን ደረጃ ይመረጣሉ?
ሕክምናው በየትኛው የአለማችን ክፍል ይሰጣል? ...ወዘተ
ከላይ የተጠቀሱትን ጥያቄዎችና ሌሎችንም ዶ/ር ዮናስ ተስፋሁን በናይን የእናቶችና የህጻናት ሆስፒታል የጽንስና ማህጸን ሐኪም ያብራሩልናል፡፡
ጥ/    የማህጸን ኪራይ ሲባል ምን ማለት ነው?
መ/    የማህጸን ኪራይ የሚለው ቃል በሕክምናው ሰሮጋሲ (Surrogacy) ተብሎ ይጠራል፡፡ ማህጸናቸውን የሚያከራዩ ሴቶች ደግሞ (Surrogate mothers) ሰሮጌት እናቶች ተብለው ይጠራሉ፡፡ የማህጸን ኪራይ ማለት ጥንዶች ልጅ መውለድ ባይችሉ እና የልጅ አለመውለዳቸው ምክንያት ደግሞ የእናትየው ማህጸን ልጅ መሸከም አለመቻል ከሆነ ይህንን ችግር ለመፍታት ወደ ማህጸን ኪራይ ይኬዳል፡፡ ማህጸንዋን የምታከራየው ሴት ልጁን በሕክምና ዘዴ በማህጸንዋ ተቀብላ ዘጠኝ ወር ድረስ በማህጸንዋ ተንከባክባና አሳድጋ የእርግዝና ጊዜው ሲያበቃ ወልዳ ልጁን ለወላጆቹ የምታስረክብ እናት ናት፡፡
ጥ/    ማህጸን ልጅን መሸከም የማይችልበት ምክንያት ምንድነው?
መ/    በሕክምናው ዘርፍ የሚጠቀሱ ማህጸንን ጽንስ እንዳይሸከም የሚያደርጉ የተለያዩ የጤና ምክንያቶች አሉ፡፡
1/ አንዳንድ ሴቶች ሲፈጠሩ ጀምሮ ማህጸናቸው ጽንስ መሸከም የማይችል ሆኖ ሊፈጠር ይችላል። አንዳንድ ሴቶች ደግሞ ማህጸንቸው ቢኖርም ልጅን ለማርገዝ ወይንም ለማቀፍ የሚረዳው የውስጠኛው ክፍል ማለትም Endometrium የሚባለው በተፈጥሮው የማይዳብር የማያድግ ሊሆን ይችላል፡፡
በተለያዩ በሽታዎች ምክንያት ሴቶች ማህጸናቸውን ሲያጡ በማህጸን እጢ ወይንም ደም በከፍተኛ ሁኔታ እንዲፈሳቸው የሚያደርግ የማህጸን በሽታ፣
በወሊድ ወቅት በተከሰቱ አንዳንድ ችግሮች ሳቢያ ወይንም በሌላ ምክንያት ማህጸናቸው እንዲወጣ ከተደረገም ማህጸናቸው ልጅ ሊሸከም ስለማይችል ማርገዝ አይችሉም፡፡
2/ ከውርጃ ወይንም ከመውለድ፣ ከኦፕራሲዮን ጋር በተያያዘ አንዳንድ ተላላፊ ኢንፌክሽኖች ማህጸንን በሚጎዱበት ጊዜ ማህጸን ላይ ከፍተኛ የሆነ ጠባሳ ስለሚፈጠር ይህ ጠባሳ ደግሞ የማህጸንን የውስጠኛውን ግድግዳ ልጅ ለመሸከም ብቁ እንዳይሆን ያደርገዋል፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚነሳ ሌላው ችግር ተደጋጋሚ ውርጃ ነው፡፡
3/ ሌላው ችግር የውስጥ ደዌ ነው፡፡ ሴቶች ለደም ግፊት፣ ስኩዋር፣ የኩላሊት ሕመም የመሳሰሉት ችግሮች ካሉባቸው ልጅ አርግዞ መውለድ ለእናትየው ሕይወት አስጊ ስለሚሆን እንዲያረግዙ አይመከርም፡፡ አስቀድሞ በሕክምና መከላከል ካልተቻለ ውጤቱ አስከፊ ነው፡፡
ጥንዶች አንዳንድ ጊዜ በሰው ሰራሽ ዘዴ ሊወልዱ የማይችሉበት አጋጣሚም ይኖራል፡፡ በተለይም እናትየው እድሜዋ ገፋ ያለ ከሆነና በሰው ሰራሽ ዘዴ የተዳቀለውን ጽንስ ማህጸንዋ ማሳደግ ካልቻለ የግድ ማህጸን የምታከራይ ሴት አስፈላጊ ትሆናለች፡፡
ጥ/    በእራስዋ ተፈጥሮአዊ ሒደት ለማርገዝ ያልተዘጋጀች ሴት በማህጸን ኪራይ ለምታረግዘው ልጅ ምን ያህል ተፈጥሮአዊ ሁነቶችን ታሟላለች?
መ/    ማህጸናቸውን የሚያከራዩ ሴቶች ማህጸናቸውን ከማከራየታቸው በፊት የሚያካሂዱአቸው አንዳንድ የጤና ምርመራዎች አሉ፡፡ ይህ የጤና ምርመራ ለልጁ ተላላፊ በሽታ እንዳትሰጠው (ኤችአይቪ፣ አንዳንድ ቫይረሶች…) እንዳይኖሩ ሙሉ የጤና ምርመራ ታደርጋለች፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ይህች ማህጸንዋን የምታከራይ ሴት ልጁ በማህጸንዋ ውስጥ ማደግ የሚችል መሆን ያለመሆኑን በማህጸን ምርመራ እንዲረጋገጥ ይደረጋል፡፡ ከዚያም በሁዋላ ይህች ሴት ከውጭ የሚዘጋጀውን ጽንስ ከመቀበሉዋ በፊት የሚሰጣት አንዳንድ ሕክምናዎች አሉ፡፡ የመጀመሪያው ደረጃም የወር አበባዋ በሕክምና ዘዴ ቁጥጥር ውስጥ እንዲገባ ማድረግ ነው፡፡ ሆርሞኖችን በማዘጋጀት እንድትወስድ በማድረግ የወር አበባዋን ዑደት ካስተካከሉ በሁዋላ የማህጸንዋ የውስጠኛው ግድግዳ ጽንስን እንዲቀበል በማዘጋጀት ከጥንዶች የተወሰደውን ዘር በህክምና ዘዴ በማዳቀል ጽንስ ለመፈጠር ምቹ ሁኔታ ሲኖር ወደማህጸንዋ በማስገባት እንዲያድግ ይደረጋል፡፡ ሁሉም ነገር በጥንቃቄ የሚካሄድ በመሆኑ የሚፈጠረው ልጅ ሊያገኘው የሚገባውን ተፈጥሮአዊ በረከቶች ምንም አያጣም፡፡
ጥ/    የማህጸን ኪራይ ስንት አይነት ነው?
መ/    ሁለት አይነት የማህጸን ኪራይ አለ፡፡ አንደኛው ማህጸንን ብቻ ማከራየት ሲሆን ሌላኛው ግን ማህጸንን ብቻ ሳይሆን ማህጸን የምታከራየው ሴት ዘር የምትሰጥበት አካሄድ አለ፡፡ ሁለተኛው አይነት የማህጸን ኪራይ የሚያገለግለው አባትየው ዘር ኖሮት እናትየው ግን ምንም አይነት ዘር የማይኖራት ሲሆን ነው፡፡ ከወንድየው የተገኘውን ዘር በሕክምና ዘዴ በሴትየዋ ማህጸን ውስጥ በመርጨት አንዳንድ ጊዜ ተፈጥሮአዊ በሆነ መልኩ ልጅ እንዲወለድ ይደረጋል፡፡ በሌላኛው የማህጸን ኪራይ ሂደት ግን ማህጸን የምታከራየው ሴት የእራስዋ እንቁላሎች ስለሚኖሩዋት ያንን የእራስዋን እንቁላል የወር አበባዋን በመቆጣጠር እና እንዲታገድ በማድረግ ማህጸንዋን በተለያዩ ሕክምናዎች በማዳበር ብቻ ጽንስ ለመቀበል ዝግጁ መሆኑ ታይቶ የተዘጋጀውን ጽንስ ወደማህጸንዋ በማስገባት እንዲያድግና እንዲወለድ ይደረጋል፡፡
ጥ/    የወር አበባ ማየት ያቋረጠች ሴት ማህጸን ማከራየት ትችላለች?
መ/    ማህጸንን በማከራየት አሰራር የተቀመጡ መመዘኛዎች አሉ፡፡ ብዙ ጊዜ የወር አበባ ማየት ያቆመች ሴት ማህጸንዋን እንድታከራይ አይፈቀድም። የዚህም ምክንያት ማርገዝ በራሱ የተለያዩ ችግሮችን ሊያስከትል ስለሚችል ነው፡፡ እርግዝና ከስነልቡና እንዲሁም ከአካላዊ ጤንነት እና ብቃት ከመሳሰሉት ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊደረግለት የሚገባ በመሆኑ ማህጸንን ማከራየት የሚፈቀደው በእድሜ ገፋ ባላሉና በተለይም በመውለጃ እድሜ ላይ ላሉት ነው፡፡ በእርግጥ እንደ ህክምናው ሲታይ ማህጸኑን ማዘጋጀትና ጽንስ እንዲቀበል ማድረግ ይቻል ይሆናል፡፡ ግን ውጤቱ አሳሳቢ ነው፡፡ ስለሆነም ብዙ ጊዜ ማህጸንን የሚያከራዩ ሴቶች እድሜያቸው እስከ ሰላሳ አመት ወይንም ከዚያ በታች ቢሆን ይመረጣል፡፡
ጥ/    ሕክምናው በየትኞቹ የአለም ክፍሎች ይሰጣል?
መ/    የማህጸን ኪራይ ሕክምናው ረቀቅ ያለና ወጪውም ከፍ ያለ ነው፡፡ ስለሆነም በአፍሪካ ውስጥ እስከአሁን ድረስ የማውቀው ነገር የለም፡፡ ባደጉት አገሮች ውስጥ ግን ብዙዎችን ልጅ ለማቀፍ ያበቃ ቴክኖሎጂ ነው፡፡  በቅርብ እርቀት ካሉት አገሮች ሕንድ አገር ውስጥ የህክምናው ዘዴ በጣም እያደገ በመምጣቱ በሰው ሰራሽ ዘዴ ማርገዝ እንዲሁም የማህጸን ኪራይ እና የመካንነት ችግሮችን የሚመለከት ሕክምና ይሰጣል፡፡ በሕንድ አገር በድህነት የሚኖሩ ብዙ ሴቶች ማህጸናቸውን በማከራየት ከድህነት ለመላቀቅ ጥረት የሚያደርጉም አሉ፡፡ በተረፈ የቀድሞ ሶቭየት ህብረት አገሮች፣ እንግሊዝ፣ አሜሪካ የማህጸን ኪራይ በህግ የተፈቀደ በመሆኑ አገልግሎቱ በመሰጠት ላይ ነው፡፡
ጥ/    የማህጸን ኪራይን የሚከለክሉ አገሮች አሉ?
መ/    የማህጸንን ኪራይ የሚከለክሉ አገሮች አሉ። ይህም ከተለያዩ ባህላዊ እና ሀይማኖታዊ ምክንያቶች ከመሳሰሉት መነሻነት ሲሆን ብዙዎቹን እናትነት የሚለው ነገር የሚያነጋግራቸው ጉዳይ ነው፡፡ አንዲት ሴት ልጅ ማህጸንዋ የእስዋ ስለሆነ ማከራየት ትችላለች ወይ? የልጁ እናት አርግዛ አምጣ የወለደችው ናት ወይንስ ዘር የሰጡት ናቸው? በሚለው ላይም የሚከራከሩ አሉ፡፡
ጥ/    የማህጸን ኪራይ አሰራር በምን መልክ ጥንቃቄ ይደረግለታል?
መ/    በማህጸን ኪራይ አሰራር ላይ የሚደረግ ብዙ ጥንቃቄ አለ፡፡ ይህ አሰራር ብዙ ባለሙያዎችን የሚያሳትፍ ነው፡፡ የማህጸን ህክምና ባለሙያዎች፣ የውስጥ ደዌ ሐኪሞች፣ የህግ ሰዎች፣ የስነልቡና ባለሙያዎች አንድ ላይ በመሆን ነው ስራውን የሚሰሩት። አንዳንድ ጊዜ በኪራይ ጽንስ ከጸነሱ በሁዋላ ልጁ ሲወለድ ለመስጠት የማንገራገር ነገር ሊኖር ስለሚችል ብዙ ማሰሪያ አለው፡፡ በእርግጥ በሕክምናው ዘርፍ እናትነትን በተለያዩ መንገዶች ይገልጹታል፡፡ ከልጁ ጋር ምንም አይነት የዘር ግንኙነት ሳይኖራት የወለደችውም እንደ እናት ትቆጠራለች፡፡ ዘር ያዋጣችውም እናት ነች። ስለዚህ የእናትነት ትርጉሙ በሚፈጠሩት ልጆችም ላይ ውዥንብር ሊፈጥር ስለሚችል አሰራሩ ጥንቃቄ የተሞላበት ነው፡፡
ጥ/    የህክምናው ተስፋ በኢትዮጵያ ምን ይመስላል?
መ/    በእርግጥ የሚቀድመው ጥንዶች ልጅ መውለድ ካልቻሉ በህክምናው በመታገዝ የሚወልዱበትን ዘዴ ለማመቻቸት የሚደረገው ጥረት ነው፡፡ በኢትዮጵያ የማህጸን ኪራይ ህክምናን ለመጀመር የህግ ማእቀፍ …ስነምግባር የመሳሰሉት አስፈላጊ በመሆናቸው በቅርብ ጊዜ ይጀመራል የሚል እምነት የለኝም፡፡

Published in ላንተና ላንቺ
Page 8 of 16