“ባለሀገሩ አስጐብኚ ድርጅት” አባት አርበኞችን ወደ ታላቁ ህዳሴ ግድብ ወስዶ ለማስጐብኘት እየተንቀሳቀሰ ነው
“ግድቡን ጠዋት ጐብኝቼ ማታ ብሞት ገነት እንደምገባ እርግጠኛ ነኝ” - አባት አርበኛ
ትክክለኛ ስሙ ተሾመ አየለ ቢሆንም ብዙዎች “ባለሀገሩ” በሚል ስያሜው የበለጠ ያውቁታል፡፡ ዘወትር በሚለብሰው ባህላዊ ልብስና በሚያጎፍረው ፀጉሩ ይታወቃል። በድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) “ጥቁር ሰው” የሙዚቃ ቪዲዮ ላይ የባልቻ አባነፍሶን ገፀ-ባህሪ ወክሎ በመጫወት ብዙዎችን አስደምሟል። “ባላገሩ” የተሰኘ የአገር ውስጥ አስጐብኚ  ድርጅት ከፍቶ በመስራት ላይም ይገኛል። በቅርቡ በቶቶት ሆቴል በተዘጋጀ የባህል ልብሶች የመልበስ ውድድር ከተሸላሚዎቹ አንዱ ሆኗል - ወጣት ተሾመ አየለ፡፡
ባለፈው ማክሰኞ ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ፤ 50 ለሚሆኑ አርበኞች የታላቁን ህዳሴ ግድብ ለማስጎብኘት ማቀዱን ተናግሯል፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ በቱሪዝም፣ በሥራ ተመክሮውና በህይወቱ ዙርያ አነጋግራዋለች፡፡

ባላገር ነኝ፤ ንግግር አልችልም ስትል ሰምቼ ነበር፡፡ ትውልድና እድገትህ የት ነው?
ትውልድና እድገቴ በሰሜን ሸዋ አካባቢ፣ ደብረ ብርሃን ዙሪያ፣ ወረዳ በዞ የሚባል ቀበሌ ውስጥ ነው።
እንዴት ወደ አዲስ አበባ መጣህ? የትምህርትህስ ሁኔታ ምን ይመስላል?
ትምህርቴን የተማርኩት እስከ 10ኛ ክፍል ነው። ነገር ግን አሁን በምሰራበት የቱሪዝም ሙያ ዙሪያ የተለያዩ የቱሪዝም ስልጠናዎችን ወስጃለሁ፡፡ አዲስ አበባ ከገባሁ ወደ 12 ዓመት ሆኖኛል፡፡ አዲስ አበባ መጥቼ ስራ የጀመርኩት በጣም አነስተኛ በሚባል ደሞዝ ነበር፡፡
አነስተኛ ስትል ስንት ብር ነው? ስራውስ ምን ነበር?
ደሞዙ በወር 35 ብር ሲሆን ስራው ዘበኝነት ነበር። ማታ ዘበኝነት እሰራለሁ፤ ቀን ቀን ደግሞ የጉልበት ስራ፣ ሸክም እየተሸከምኩ  መንጃ ፍቃድ ለማውጣት ገንዘብ እቆጥብ ነበር፡፡ ቁርስ በልቼ ከሆነ ምሳ ወይም እራት በመዝለል ነበር ገንዘብ የምቆጥበው፡፡ ያንን ካላደረግሁ ትልቅ ቦታ እንደማልደርስ አውቅ ነበር። ህይወት እንደጠበቅኩት ባለመሆኑ እንጂ አዲስ አበባ የመጣሁት ለመስራት ሳይሆን ለመማር ነበር፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች ግን መማር አልቻልኩም፡፡
መንጃ ፍቃዱን አወጣህ?
የእግዚአብሄር ፈቃድ ተጨምሮበት እኔም ታግዬ መንጃ ፈቃዴን አወጣሁ፡፡ በቢጂአይ ኢትዮጵያ በቢራ ጫኝ እና አውራጅነት ተቀጥሬ እሰራ ነበር። በኋላ ላይ መንጃ ፈቃድ ስለነበረኝ  በሹፍርና ተቀጠርኩ፡፡ ከዚያ የሽያጭ ባለሙያ ሆንኩኝ፡፡
ለምንድነው ብዙ ሰዎች “ባላገሩ” እያሉ የሚጠሩህ?
ስራዬን በአግባቡ ስለምሰራ አለቆቼ ይወዱኝ ነበር፡፡ ታዲያ አብረውኝ የሚሰሩት ባልደረቦቼ “ይሄ ቆምጬ ባላገር እኮ እኛን አሳጣን” ይላሉ፡፡ በዚያው ባላገር እያሉ መጣራት ጀመሩ፡፡ እኔም አልከፋኝም። እውነትም ባላገር ነኝ፡፡ ባላገር ማለት አገር ያለው ማለት ነው፡፡ “ትናንትና ከእረኝነት መጥቶ ዛሬ እኛን በለጠን፤ ይሄ ባላገር ዶሮ ጠባቂ” ይሉኝ ነበር።  ባላገር ማለት ወግ ማእረግን አክብሮ የሚኖር፤ የሚታረስ ቦታ፣ የሚኖርበት ስፍራ፣ የሚከበርበት ባህልና ትውፊት ያለው ማለት ስለሆነ፣ ባላገርነቴን ተቀብዬው ኮርቼበት እኖራለሁ፡፡ በአጠቃላይ ባላገር ማለት በእርሻ አገሩን አልምቶ፣ አገሩን የሚመግብ የአገር ዋልታ ማለት ነው፡፡
እንዴት ነው ወደ ቱሪዝም ዘርፍ ልትገባ የቻልከው? “ባላገሩ አስጎብኚ” ድርጅትን እንዴትና መቼ አቋቋምክ?
ወደ ቱሪዝም ሥራ ለመግባት አጋጣሚው የተፈጠረልኝ በ1997 ዓ.ም መጨረሻ ላይ ነው፡፡ የአፍሪካ ህብረት ጉባኤ በተካሄደበት ወቅት የዘመዴን መኪና የሊቢያ ኤምባሲ ተከራይቶት ሰለነበር እሱ ላይ እሰራ ነበር፡፡ በወቅቱ እኔ የማውቃቸው የእንግሊዝኛ ቃላት ቢቆጠሩ 15 አይሞሉም ነበር፡፡
እስከ 10ኛ ክፍል ተምረህ የለም እንዴ? እንዴት 15 አይሞሉም፤ ቢያንስ 150 እንኳን መሆን ነበረባቸው …
(ሳ….ቅ) ያው ትምህርት አቋርጠሽ ለረጅም ጊዜ ሌላ ስራ ስትሰሪም ይረሳል እኮ! የሆኖ ሆኖ እዚያ ስሰራ የቱር ባለቤቶች ሸራተን አገኙኝ፡፡ መኪናውንም ወደዱት፤ መከራየት ጀመሩ፡፡ ያለኝን የስራ ፍቅር፣ ትህትናዬን ያዩ የኤፍኬ አስጎብኚ ድርጅት ባለቤት አቶ ፍቅረሥላሴ፤ “ለቱሪዝም የሚመጥን ባህሪ ስላለህ ከዚህ ሥራ ባትወጣ ጥሩ ነው” የሚል ምክር ሰጡኝ። ከዚያም በራሳቸው ድርጅት ስልጠና ሰጥተውኝ፣ ባዶ መኪና ይዤ፣ ቱሪስቶች ተከትዬ እየሄድኩ ልምድ እንዳዳብር ካደረጉኝ በኋላ፣ ብቃቴን አረጋግጠው ከእሳቸው ጋር ለረጅም ጊዜ ሰራሁ፡፡ ከዚያም ለውጥ ስለሚያስፈልግ በሌላ ድርጅት ውስጥ ተቀጠርኩ። ከሁለት ዓመት በፊት ደግሞ “ባላገሩ አስጎብኚ” በሚል የአገር ውስጥ ጎብኚዎች ላይ ትኩረት ያደረገ የራሴን ድርጅት ለመክፈት በቃሁ፡፡
በምን ያህል በጀት ነው ድርጅትህን የከፈትከው?
ምንም ገንዘብ አልነበረኝም!! በሶስትና አራት ድርጅቶች ተቀጥሬ የቱር ስራ ስሰራ የቆጠብኩት ገንዘብ አልነበረኝም፡፡ በነገራችን ላይ ቱሪዝም ማለት ለእኔ ፍቅር ነው፤ ህይወትሽን ሰጥተሸ ልትሰሪው የሚገባ ስራ ነው፡፡ ገጠር ውስጥ እንግዳ ሲመጣ ጎንበስ ቀና ብለሽ፣ እግር አጥበሽ፣ ቤት ያፈራውን አቅርበሽ፣ ፊትሽን በፈገግታ አድምቀሽ ነው የምትቀበይው፡፡ ይሄ ቱሪዝም የሚፈልገው ትክክለኛ ባህሪ ነው፡፡ ይህ ባህሪ ደግሞ በትምህርት ሳይሆን በአስተዳደግና ካደግሽበት ማህበረሰብ የምትወርሺው ነው፡፡ በዲግሪ በማስተርስ ይመጣል ብዬ አላስብም፡፡ የሆነ ሆኖ ብር ያላጠራቀምኩበት ዋና ምክንያት፣ ልናስጎበኝ ስንሄድ የምወስዳቸው እንግዶች ቢታመሙ፣ አንድ ነገር ቢደርስባቸው በቅርብ ለመገኘት ስል እነሱ የሚያርፉበት ውድ ሆቴል  ስለማድርና አበሌን ለሆቴልና ለምግብ ከፍዬ ባዶ እጄን ወደ ቤቴ ስለምመለስ ነበር፡፡
ታዲያ አስጎብኚ ድርጅትን ያህል ትልቅ ተቋም በምን ካፒታል ከፈትክ?
በመጨረሻ ላይ የሰራሁበት ድርጅት አንድ መኪና ተበላሽቶብኝ ከስራ ስቀነስ፣ በባንክ ሂሳቤ የነበረኝ ገንዘብ 1842 ብር ብቻ ነበር፡፡ ይህን ብር ይዤ ነው “ባለሀገሩ አስጎብኚ” ድርጅትን የከፈትኩት፡፡ ከተቋቋመ ሁለት አመቱ ነው፤ ስራውን አውቀዋለሁ፤ ፍቅር የሆነ ስራ ነው፤ ስራውን ስትሰሪ ሆቴሎች ታውቂያለሽ፤ ብዙ ግንኙነት ትፈጥሪያለሽ፤ ስለዚህ በዱቤ መስራት ይቻላል። ብድርም ታገኚያለሽ፡፡ ለስራዬ ስኬት ባለቤቴ፣ እህቶቼና አጎቴ ትልቅ አስተዋፅኦ አድርገውልኛል፡፡ ገንዘብ አበድረውኛል፡፡ አዲ ብድርና ቁጠባም ወደ 300 ሺህ ብር ገደማ አበድሮኛል፡፡ አምስት ቋሚና 18 ገደማ የኮሚሽን ሰራተኞች አሉት፤ ድርጅቱ፡፡ ትኩረት ያደረግነው ሎካል ቱሪዝም (የአገር ውስጥ ጐብኚዎች) ላይ ነው፡፡ በአገራችን አገርን የመጎብኘት ባህላችን ደካማ በመሆኑ ሳዝን ኖሬያለሁ፡፡ አሁን ግን ትኩረት ያደረግነው ዜጎች ስለአገራቸው በደንብ እንዲያውቁና እንዲጎበኙ ማድረጉ ላይ ነው። ኢትዮጵያን ለነጭ ጎብኚዎች ትተን መቀመጥ የለብንም፡፡ እነሱም አጠራቅመው እንጂ ተርፏቸው አይደለም የሚጐበኙት፡፡
በአሁኑ ወቅት አንድ ሰው ሁለት ማኪያቶ የሚጠጣ ከሆነ አንድ እየጠጣ፣ የተወሰነ መንገድ በእግሩ በመሄድ የትራንስፖርት ወጪውን ቀንሶ፣ በቀን አስር ብር፣ በወር 300 ብር፣ በአመት 3600 ብር በመቆጠብ፣ በጋራ ሰብሰብ ብሎ አገርን የመጎብኘት ልምድ እንዲያዳብር ግንዛቤ የማስጨበጥ ሥራ እየሰራን ነው፡፡
በሁለት አመት ውስጥ ምን ያህል የአገር ውስጥ ጎብኚዎችን አስተናግዳችኋል?
ባለፈው አመት 1ሺህ ዘጠኝ መቶ ጐብኚዎችን አስተናግደናል፡፡ ዘንድሮም ተቀራራቢ ቁጥር ያላቸው የአገር ውስጥ ጎብኚዎች ያስተናገድን ሲሆን አሁን የውጭ ጎብኚዎችንም ማስተናገድ ጀምረናል። ግንኙነቶችን እየፈጠርን ነው፡፡ ፍላጎት እያሳዩ ያሉ ጎብኚዎች አሉ፡፡ ሶስት ጥሩ ጥሩ የጉዞ መኪኖችም አሉን፡፡
ወደ አለባበስህ እንምጣ፡፡ 365 ቀናት የአገር ባህል ልብስ ነው የምትለብሰው፡፡ ፀጉርህን እንደ አርበኞች አጎፍረህ በማበጠርም ትታወቃለህ፡፡ መቼ ነው የጀመርከው?
ተወልጄ ያደግሁት ገጠር እንደመሆኑ፣ አዲስ አበባ እስክመጣ በባህል ልብስ ነው ያደግሁት፡፡ አዲስ አበባ ከመጣሁ በኋላ አጎቴና እህቶቼ የገዙልኝ ዘመናዊ የፈረንጅ ልብስ ከሰውነቴ ጋር ሊዋሀድ አልቻለም፡፡ ሱፍ ለብሼ አየሁት፤ አልተስማማኝም፣ ጂንስ ለበስኩኝ፤ መራመድ አልቻልኩም፡፡ ስለዚህ ለእኔ የተፈጠረ አይደለም አልኩና ወደ አሳደገኝ ቁምጣዬ ተመለስኩኝ፡፡ ከተወለድኩ ጀምሮ እስካሁን በአገሬ ባህል ልብስ ነው የምዋበው፤ የፈረንጅ ልብስ ለብሼ አላውቅም፤ የመልበስ ፍላጎትም የለኝም፡፡
አርበኞችን ወደ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ወስዶ የማስጎብኘት ሀሳብ የተጠነሰሰው እንዴት ነው?
እንደሚታወቀው ኢትዮጵያ ከአፍሪካ አገራት ብቸኛዋ ቅኝ ያልተገዛች አገር ናት፡፡ በዚህም እንኮራለን፡፡ ለዚህ ኩራታችን ዋነኛ ባለውለታዎች ደግሞ የኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ናቸው፡፡ ለዚህ ኩራት፣ ነፃነትና ክብር ህይወት አልፏል፤ ደም ፈስሷል፤ አጥንት ተከስክሷል፡፡ በአንድ አጋጣሚ አንድ አባት አርበኛ ያገኙኝና “አሁን 94 አመት ሆኖኛል፤ በተለያየ ጊዜ የነበሩ ትውልዶች የተለያየ ገድል ሰርተው አልፈዋል፤ ይሄኛው ትውልድ ደግሞ የዘላለም ቁጭቴ የነበረውን የአባይን ግድብ እየገነባ ነው፡፡ እኔ ግድቡን ጠዋት ጎብኝቼ ማታ ወይም
በነጋታው ብሞት ቀጥታ ገነት እንደምገባ እርግጠኛ ነኝ፤ እህ የእኔ ልጅ፤ ይህን ብታደርግ አንተንም መርቄህ አልፋለሁ” አሉኝ፡፡ ጉዳዩን ከስራ ባልደረቦቼ ጋር ተመካክረንበት፡፡ ለምን በመኪና የምንችለውን ያህል ወስደን አናስጎበኛቸውም የሚል ሀሳብ ላይ ደረስን፡፡ ከዚያም ከጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር ጋር ተነጋገርን፤ ሀሳቡ ጥሩ ነው በሚል ድጋፍ ሰጡን፡፡ መጀመሪያ በኛ ደርጅት የሚሳካ መስሎን ነበር፡፡ በትንሹና በህፃኑ ድርጅታችን የምንሰራው ከሆነ ግንጥል ይሆናል በሚል፣ ጉዳዩ አገራዊ ይዘት እንዲኖረው ለማድረግ ወሰንን፡፡
በመግለጫው ላይ እንደተባለው ወደ 77 ያህል ተጓዦች ይሳተፋሉ፤ በጀቱም ወደ አንድ ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ነው፡፡ በእርግጠኛነት የሚሳካ ዕቅድ ይመስልሃል?
እኛ እንዲሳካ የሚቻለውን ሁሉ እናደርጋለን። በሄሊኮፕተር ወስደን ብንመልሳቸው መልካም ነው። ይሄ እንግልትን ይቀንሳል፡፡ ምክንያቱም ትንሹ እድሜ የሚባለው 85 ዓመት ነው፡፡
ሁሉም ከዚያ በላይ እስከ 96 ዓመት እድሜ ያላቸው ናቸው፡፡ እነዚህ አባቶች ዶክተርና ነርሶች አብረዋቸው የሚጓዙ ቢሆንም እንግልቱን መቀነስ አለብን፡፡ በአንድ ቀን ግድቡን ጐብኝተው በዚያው ቀን ቢመለሱ ይሻላል፡፡ ለዚህም ሄሊኮፕተር የምንከራይበትን አሊያም በነፃ የምናገኝበትን መንገድ እየፈለግን ነው፡፡
እስካሁን ድጋፍ ለማድረግ ፈቃዳቸውን ያሳዩ ድርጅቶች አሉ?
ለኢትዮጵያ አየር መንገድና ለመከላከያ ሚኒስቴር ደብዳቤ ፅፈን ተስፋ ሰጪ ነገሮችን አይተናል፡፡ የትኛውም ኢትዮጵያዊ ካለው ላይ ቀንሶ በመስጠት፣ የአርበኞችን ምኞት እውን ያደርግልናል የሚል ተስፋ አለን፡፡ የአባቶች ወደ አባይ መሄድ፣ እዚያ በበረሀ ግድቡን በፅናት  የሚሰሩ ኢትዮጵያዊያንን ሞራል ይገነባል፡፡ አባቶችም ምርቃት ይሰጣሉ። አባቶች ከጉብኝት በኋላ አዲስ አበባ ተመልሰው ምስክርነት ሲሰጡ ህዝቡ ለግድቡ ብር የማዋጣት ፍላጎቱ ይጨምራል፡፡ የአንዳንድ “አማርኛ ተናጋሪ ግብፃዊያንንም” አንገት ያስደፋል፡፡ እስከ መጪው መስከረም ሶስት ድረስ የጉብኝት ጉዞው በትክክል እንደሚሳካ እምነቴ ነው፡፡ እስካሁን በእጃችን የገባ ገንዘብ የለም፡፡ ግን ይሳካል፡፡
በመግለጫህ ላይ 77 ተጓዦች በጉብኝቱ እንደሚካተቱ ገልፀሃል፡፡ እነማን ናቸው?
50 አርበኞች፣ 16 የተለያዩ ሚዲያ ጋዜጠኞች፣ 6 ከአባቶች የአደራ ቃል የሚረከቡ የመንግስት ባለስልጣናት፣ አንድ ዶክተርና አንድ ነርስ፣ ሁለት አዝማሪዎች፣ ሁለት አስተባባሪዎች፣ በድምሩ 77 ተጓዦችን ያካትታል፡፡

ከአምስት አመታት በፊት…
ከታቦር ተራራ እስከ አላሙራ ጋራ፣ ጉም ጭጋግ የለበሰች… ከአረብ ሰፈር እስከ ፒያሳ፣ በካፊያ የረሰረሰች የቆፈነናት ሃዋሳ…
ካፊያው እስኪያቆም ለመጠበቅ የሚያስችል እንጥፍጣፊ ትዕግስት ያጣን፣ ሁለት ቸኳይ መንገደኞች፣ ከአሞራ ገደል ወደ ፒያሳ የሚያቀናውን መንገድ ተከትለን፣ ነጠቅ ነጠቅ እያል እንጓዛለን - ጋሽ መስፍኔና እኔ፡፡
ፒያሳ ለመድረስ ቸኩለናል፡፡ እዚያ ነው፣ ከሃዋሳ ልጆች ጋር ልንገናኝ የተቀጣጠርነው። በሰዓቱ ለመድረስ አስበን፣ ከፍቅር ሃይቅ ቀደም ብለን ብንነሳም፣ ድንገት መጣል የጀመረው ዝናብ ግን እንቅፋት ሆነብን፡፡ በየጥጋጥጉ እየተጠለልን ልናሳልፈው ብንሞክርም፣ ሄድ መጣ እያለ ጉዟችንን አስተጓጎለው፡፡
በስተመጨረሻም እስኪያባራ ከመጠበቅ፣ ፈጠን ብለን መጓዝ እንደሚሻለን ተስማምተን፣ ብርድ የሚያስረሱ የልጅነት ዘመን ትዝታዎቹን እያስኮመኮመኝ በካፊያ ውስጥ መራመዳችንን ቀጠልን፡፡ በፍጥነት… ከሩጫ በማይተናነስ እርምጃ…
መካከል ላይ…
“እኔ እምለው ጋሼ… ‘የቆንጆ ልጅ ፈተና’ የሚለውን ግጥም፣ ዩኒቨርሲቲ መምህር ሆነህ ነው የጻፍከው?” ስል ጠየቅኩት፡፡
መልስ አልነበረም፡፡
ከጎኔ ሲጓዝ የነበረው ጋሽ መስፍኔም ከአጠገቤ አልነበረም፡፡
ደንገጥ ብዬ ወደኋላዬ ዞርኩ፡፡ ጋሽ መስፍኔ ጉዞውን አቋርጦ ቆሟል፡፡ ካፊያ እያበሰበሰው አይኖቹን አንድ ቦታ ላይ ተክሎ ቆዝሟል፡፡ እዚያ ቦታ ላይ ፈረስ ቆሟል፡፡
አጥንቱ የገጠጠ… ጀርባው የተላላጠ… ከስቶ የመነመነ… አይኖቹን የጨፈነ… ቋንጃዎቹ የታጠፉ… ጋማዎቹ የረገፉ… ፈራርሶ ሊወድቅ የደረሰ የቆፈነነው አሮጌ ፈረስ፣ ሞትና ህይወትን በሚያዋስነው ቀጭን ድንበር ላይ እግሮቹን ተክሎ፣ የግንብ አጥር ተከልሎ ይንቀጠቀጣል፡፡ ከመላ አካላቱ ትኩስ ጭስ ሽቅብ ይትጎለጎላል፡፡
“እስኪ አስበው አንተነህ!...” አለኝ ጋሽ መስፍን፣ በትካዜ ተውጦ ፈረሱን አሻግሮ እያየ፡፡
“እስኪ አስበው!... ይሄ የተላላጠ ደካማ ፈረስ፣ በጉብዝናው ወራት የነበረውን ግርማ ሞገስ እስኪ አስበው፡፡ ድካም ሳይጎበኘው፣ ህመም ሳያገኘው፣ እርጅና ሳይጥለው፣ ዕድሜ ሳያዝለው… ይህ ሁሉ ሳይሆን በፊት የነበረውን ጉልበት፣ የነበረውን ውበት እስኪ አስበው!... ዘመን አቅሙን ሳያደቀው፣ ጡንቻውን ሳይሸመቅቀው፣ ህመም ጉልበቱን ሳይነጥቀው፣ ጌታውም አረጀ ብሎ ከጋጣው ፈትቶ ሳይለቀው…. እንዲህ ሳይሆን በፊት፣ እንዴት እንደነበር እስኪ አስበው!...” ፈረሱን እያየ ሃዘን በሰበረው አንደበት፣ የድራማ የሚመስል ግን የገሃድ እና የልብ የሆነ ንግግሩን ቀጠለ፡፡
ፈረሱን ባለበት ትተነው ወደ ፒያሳ ስንጓዝም… ከሃዋሳ ወዳጆቻችን ጋር ደማቋን የቅዳሜ ተሲያት ስናሳልፍም፣ ወደ ደቡብ ከዘለቀው የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር የተጓዦች ቡድን ጋር ወደ አዲስ አበባ ስንመለስም… ከዚያ በኋላም፣ የጋሽ መስፍኔ ንግግርና የፈረሱ ገጽታ አብረውኝ ነበሩ፡፡
ስለፈረሱና ስለፈረስ ማብሰልሰሌን ቀጥያለሁ፡፡
.           .          .
በዚያች ምሽት…
አፍሪካውያን በንዴትና በቁጭት እርር ድብን ባሉባት በዚያች ምሽት… በደቡብ አፍሪካው የዓለም እግር ኳስ ዋንጫ፣ ጋና የአፍሪካን ተስፋ ለአሜሪካ አሳልፋ በሰጠችበት በዚያች አናዳጅ ምሽት… ውድድሩ በተጠናቀቀበት ቅጽበት… ስልኬ ጠራች፡፡ ወዳጄ ሌሊሳ ግርማ ነበር የደወለልኝ፡፡
“አያሳዝንም!?” አለኝ ሌሊሳ በከፍተኛ ሃዘን ተውጦ፡፡
“በጣም እንጂ!...” የጋና ሽንፈት፣ እሱንም እንደኔ እንዳሳዘነው እርግጠኛ ነበርኩ፡፡
“በጣም ያሳዝናል!... እንዴት እንደከሳ ልነግርህ አልችልም!... ደሞ ርቦታል!...” ሌሊሳ በስሜት ተውጦ ይናገራል፡፡
“ማነው እሱ?” ግራ ተጋብቼ ጠየቅሁት፡፡
“ፈረሱ!” ሲል መለሰልኝ፡፡
ጆሮዬን ተጠራጠርኩት፡፡
“ጨለማው ውስጥ ቆሞ ሳገኘው አሳዘነኝ!... እኛ ሰፈር አካባቢ ሳር ያለበት ቦታ ፈልጌ ሳስግጠው ቆይቼ፣ የማሳድርበት ቦታ ስላጣሁ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ይዤው እየሄድኩ ነው!...”
ሌሊሳን ተጠራጠርኩት፡፡
የሆነ ቅዠት ውስጥ ሳይሆን አይቀርም ስል ገመትኩ፡፡ በስልክ የጀመረልኝን የፈረሱን ታሪክ፣ በነጋታው በአካል ተገናኝተን ሲጨርስልኝ ግን፣ ግምቴ ስህተት እንደነበር ገባኝ፡፡ ከፈረሱ ጋር ስላሳለፈው ቀሪ የሌሊት ጉዞ አጫወተኝ፡፡ ፈረሱን ለፖሊስ ለማስረከብ በድቅድቅ ጨለማ ጋማውን ይዞ ያደረገውን ጀብደኝነት የተሞላበት ጉዞ ተረከልኝ፡፡
ያኔ ነው የጋሽ መስፍኔንና የሌሊሳን ፈረሶች ያዳቀልኳቸው… ‘ሰውረስ’ ብዬ የተረክኋቸው፡፡
*   *   *
ከሁለት አመታት በፊት… ጋሽ መስፍኔን መርካቶ አካባቢ አገኘሁት፡፡ “አንተነህ… ፈረሱንኮ አየሁት!” አለኝ ፊቱ በደስታ ወገግ ብሎ፡፡ እኔም አድራሻው ጠፍቶብኝ እንጂ፣ ፈረሱን ላሳየው ፈልጌ ያለበትን ማጠያየቅ ከጀመርኩ ብዙ ጊዜ ሆኖኝ ነበር፡፡“መጨረሻውን ግን አልወደድኩትም!... ፈረሱ እንደተመኘው ታቦር ተራራ አናት ላይ ወጥቶ ሳር ሲግጥ፣ ጠግቦ ሲያንፏርር፣ ከህመሙ አገግሞ ሽምጥ ሲጋልብ ማየት ነበር የምፈልገው!...” ጋሽ መስፍን በስሜት ተውጦ ነበር የሚናገረው፡፡
እውነቱን ነው!...
በ2003 ዓ.ም ለንባብ ባበቃሁት ‘መልስ አዳኝ’ የተሰኘ የአጭር ልቦለዶች ስብስብ መጽሃፌ ውስጥ ያካተትኩት “ሰውረስ” (ሰው እና ፈረስ እንደማለት) የሚል ርዕስ ያለው ታሪክ፣ ፈረሱ ገና ከህመሙ ሳያገግም… የናፈቀውን ሳር ሳይግጥ… ጋሽ መስፍኔ እንደተመኘው ታቦር ተራራ አናት ላይ ሳይደርስ ነበር የቋጨሁት፡፡
*   *   *
ጋሽ መስፍኔ…
እኔም ያንተን መጨረሻ አልወደድኩትም፡፡
ከሁለት ወራት በፊት አዲስ አድማስ ግቢ ውስጥ አግኝቼህ፣ አንድ ነገር ነግረኸኝ ነበር፡፡
“ከዚህ በፊት በጋዜጣው ላይ የታተሙትን ጽሁፎቼን አሰባስቤ ላሳትማቸው ነው የመጣሁት” ብለኸኝ ነበር፡፡
የፈረሴን መጨረሻ እንዳልወደድከው፣ እኔም ያንተን መጨረሻ አልወደድኩትም፡፡
አንተም እንደ ፈረሴ ከህመምህ አገግመህ፣ ባይህ ነበር ደስ የሚለኝ!... የእሱ ምኞት ተሳክቶ ማየት እንደሻትከው፣ እኔም ምኞትህን አሳክተህ ማየት ነበር የምፈልገው፡፡ እንደተመኘኸው ጽሁፎችህን አሳትመህ በደስታ ስትፍለቀለቅ ሳላይ፣ ታሪክህ መቋጨቱን አልወደድኩትም!...
ለነገሩ ባልወደውስ፣ የሆነውን ከመቀበል ውጭ ምን እላለሁ?!... የወጠነውን ታሪክ፣ ይሆናል ባለው መልኩ መጨረስ፤ ያስጀመረውን ጉዞ፣ በመሰለው መንገድ መቋጨት… እሱ የ‘ደራሲው’ ምርጫ ነው!... ባይሆን ‘ክፍል ሁለት’ህን ያሳምርልህ!
ነፍስህን በገነት ያኑራት ጋሼ!!!

Published in ጥበብ

       አራት ኪሎ ሥላሴ ቤተክርስቲያን ግቢ የሚገኘው የመቃብር ሥፍራ ባለፉት 70 ዓመታት የበርካታ ታዋቂ ኢትዮጵያዊያን የቀብር ሥነ-ስርአት ተፈጽሞበታል። አንጋፋው ደራሲ መስፍን ሀብተማርያምም አርፎበታል፡፡
ሕልፈቱንና የቀብር ሰዓቱን ደውሎ የነገረኝ አንድ ወዳጄ “መስፍን ስለራሱ የፃፈበትን መጽሔት ይዤልህ እመጣለሁ” ባለኝ መሠረት፣ ሥላሴ ቤተክርስቲያን ቀብር ላይ ስንገናኝ ሰጠኝ፡፡ በየካቲት ወር 1988 ዓ.ም በ“ፈርጥ” መጽሔት ላይ ደራሲ መስፍን ሀብተማርያም ስለራሱ ማንነት ያቀረበውን ጽሑፍ እንደሚከተለው አሳጥሬ አቅርቤዋለሁ፡፡
ባለ ብዙ ስሞች
በሞጆ ከተማ የተወለደው መስፍን ሀብተማርያም ወላጆቹ 7 ልጆችን አፍርተው ከእንግዲህ በኋላ አንወልድም ባሉበት ሰዓት በመረገዙ እናቱ “የት ነበርክ” የሚል ሥም ሰጡት፡፡ ቤተ ዘመዱ፣ ወዳጅና ጐረቤቱም አዲሱን ሕፃን ይገልፀዋል የሚል ስያሜ መስጠት ጀመሩ፡፡ “የኋላሸት”፣ “ሲሳይ”፣ “እንግዳወርቅ”፣ “ሞጆ” ያሉትም ነበሩ፡፡ እህቱ ያወጣችለት ሥም ግን መጠሪያና መታወቂያው ሆኖ ዘለቀ፡፡
ወ/ሮ ዘቢደር የሚባሉ የእናቱ ጓደኛም “እውነቱ” የሚል ሥም አውጥተውለት እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ በዚህ ስም ጠርተውታል፡፡ ይህ መጠሪያ እንዲወጣለት ምክንያት የሆነው፤ ከአራስ ቤት ወጥቶ እናቱን ተከትሎ የተለያዩ ቦታዎች መሄድ በጀመረበት የልጅነት ዘመኑ ነው፡፡ “በልጅነቴ ሞኛ ሞኝና እልኸኛ እንደነበርኩ ትዝ ቢለኝም እውነቱን አፍረጥርጬ በመናገር እታወቅ ነበር” የሚለው መስፍን ሀብተማርያም፤ በአንዱ ዕለት እናቱና ወ/ሮ ዘቢደር እሱን ይዘው ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ይሄዳሉ። ዕለቱ የንግሥ በዓል ስለነበር፣ ታቦት ሲወጣ ሕዝቡ እልልታውን ሲያቀልጠው መስፍን ለእናቱ “ጊዮርጊስን አሳዩኝ” ይላቸዋል፡፡
እናቱ የያዙትን ጥላ ለጓደኛቸው ለወ/ሮ ዘቢደር ይሰጡና መስፍንን ከፍ አድርገው በመሸከም “ያውልህ” ይሉታል፡፡ ደጀ ሰላሙ ላይ የአባቱን ወዳጅና የእሱም ጓደኛ አባት መምሬ የምሩን ብቻ ማየት የቻለው መስፍን፤ “እኔ አሳዮኝ ያልኩት የውነቱን ጊዮርጊስ እኮ ነው” ይላቸዋል፡፡ ይህንን የሰሙት ወ/ሮ ዘቢደር ከዚያን ቀን ጀምሮ መስፍንን “እውነቱ” ብለው ባወጡለት ሥም መጥራታቸውን ቀጠሉ፡፡
ጨረቃን የሚያፈቅረው ልጅ
ተወልዶ ያደገበት የቤተሰቦቹ ግቢ ፓፓያ፣ ኮክ፣ ሮማን፣ ሸንኮራ፣ ጌሾ፣ ጫትና መሰል ፍራፍሬና አትክልቶች የሞሉበት ነበር፡፡ መስፍን ይሄን ግቢያቸውን ሲወደው ለጉድ ነበር፡፡ በልጅነቱ ሞጆ እያለ ማታ በተኛበት የዝናብ ካፊያ ቆርቆሮ ላይ ሲያርፍ መስማት፣ ምሽት ላይ ውሾችና ጅቦች የሚያሰሙት ጩኸት እንዲሁም ምሽት ላይ የምትወጣዋን ጨረቃ መመልከት ያስደስተው ነበር።
ገጣሚ ያደረገው የልዑል መኮንን ሞት
ግንቦት 4 ቀን 1949  ዓ.ም ከሞጆ በ5 ኪሎ ሜትር በሚርቅ ስፍራ ላይ ልዑል መኮንን ኃይለሥላሴ የመኪና አደጋ በገጠማቸው ማግስት፤ በሞጆ ከተማ የሚገኙ ተማሪዎች ወደ ስፍራው ሄደው ሀዘናቸውን እንዲገልፁ ተደርጐ ነበር። በዚህ ሥነ ስርዓት ወቅት ሄሊኮፕተር ይመጣና ወረቀት በትኖ ይሄዳል፡፡ ከተበተኑት አንዷን ያገኘው ልጅ መስፍን ሀብተማርያም፤ በሎሚ ዛፍ ጥላ ስር ቁጭ ብሎ በወረቀቱ የሰፈረውን ግጥም ያነባል። የሀዘን ግጥሞቹን ወደ ቤቱ ይዞ በመሄድ ደጋግሞ ካነበባቸው በኋላ፣ በማግስቱ አንድ ገጽ የሀዘን ግጥም ፃፈ፡፡ በግጥሙ ውስጥ
ያ ልዑል መኮንን የድሆች በረንዳ
ተለይቶን ሄደ ጥሎብን ብዙ ዕዳ
 የሚሉ ስንኞች ይገኙበታል፡፡ ይህንን ለአማርኛ አስተማሪው ወስዶ ሲያሳያቸው፣ “በርታ፤ ወደፊት ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ጆርናሊዝም (ጋዜጠኝነት) ትማራለህ” አሉት፡፡
ከዳይሬክተር መጽሐፍ የሚዋሰው ተማሪ
ከመደበኛ ትምህርቱ ጐን ለጐን ግጥም በመፃፍና ቴአትር ጽፎ በመተወን ይሳተፍ የነበረው መስፍን ሀብተማርያም፤ “የሰውን አነጋገር፣ አካሄድ…የመሳሰሉትን “ፎርም ማንሳት” እና የሰፈር ልጆችን ሰብስቦ ቀልድ ማሰማት፣ ያየነውን ፊልም ወይም ቴአትር አሰማምሮ እንደገና ለጓደኛና ዘመድ የማጫወት ችሎታው ነበረኝ” ሲል ፅፏል፡፡ ይህ ተሳትፎውና ታዋቂነቱ የትምህርት ቤቱ ዳይሬክተር የሚያነቧቸውን መፃሕፍት እንዲያውሱት ዕድል ፈጥሮለታል፡፡ ምፅላሉድንግል ሙሉነህ የሚባሉ የአማርኛ መምህሩም ለድርሰት ፍቅር እንዲያድርብኝ አድርገውኛል በማለት ያመሰግናቸዋል፡፡
ከድርሰት ጋር ጋብቻ የፈፀመባት አምቦ
የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን በሞጆ ካጠናቀቀ በኋላ፣ ሁለተኛ ደረጃን ለመቀጠል የሄደባት አምቦ በአማርኛና በእንግሊዝኛ የተፃፉ በርካታ መፃሕፍትን ያነበባት፤ የሥነ ጽሑፍ ዕውቀቱ ከፍ እንዲል የረዱት መምህራንን ያገኘባት፤ ጥቂት የማይባሉ ግጥሞች፣ ቴአትርና ልቦለዶችን የፃፈባት ስፍራ ሆነችለት፡፡ ስለዚያ ዘመን ሲናገር “የድርሰት ሽታው፣ መዓዛው በጭንቅላቴ መቀረጽ የጀመረው የኪነ ጥበብ ፍቅር በእድሜዬ ክልል ጉልህ ሆኖ የታየኝም አምቦ ነው” ብሏል፡፡
ከተደሰተባቸው ቀኖች በአንዱ
ደራሲ መስፍን ሀብተማርያም ስለራሱ ማንነት በየካቲት ወር 1998 ዓ.ም በፈርጥ መጽሔት ባቀረበበት ወቅት፤ ሁለት የወግና አንድ የአጭር ልቦለድ መፃሕፍትን አሳትሟል፡፡ “አዜብ” የሚል ርዕስ ያለው መጽሐፉ ታትሞ ከተሰራጨ በኋላ መጽሐፉን ያከፋፈሉለት ነጋዴዎች ትርፍህ ነው ብለው 8 ሺህ ብር እንደሰጡት ጠቅሶ፤ “በሕይወቴ የተደሰትኩበት ቀን” ብሏል፡፡ “ወይ ጉድ ለካ ገንዘብ ማለት አነስተኛም ሆኖ እንዴት ያለ የሥነ ልቦና ቶርች ነው! አጃኢብ ነው…” ሲልም ገልፆታል፡፡
ሞትን የረታባቸው መድረኮች
የ7ኛ ክፍል ተማሪ እያለ ሞጆ ከተማ በሚገኝ ወንዝ ውስጥ አምስት ሜትር ያህል ወደ ውስጥ ጠልቆ በሞት አደጋ ላይ እያለ ዋና በማይችል ጓደኛው እርዳታ ሕይወቱ ሊተርፍ ችሏል፡፡ ሁለተኛው ገጠመኝ በደርግ ዘመን በ1972 ዓ.ም የተከሰተ ነው። “እኔ የቀበሌ ጥይት በተተኮሰ ቁጥር አንድ መለኪያ እየጠጣሁ የአረቄ ጓደኛ ከመሆኔ በስተቀር እምንም ውስጥ የገባሁ አልነበርኩም” የሚለው ደራሲ መስፍን ሀብተማርያም፤ በአንዱ ዕለት አምሽቶ ወደ ቤቱ ሲሄድ በሰዓት እላፊ አሳበው ያስቆሙት ታጣቂዎች፣ አንበርክከውት የተቀባበለ መሳሪያቸውን ምላጭ ለመሳብ በተዘጋጁበት ሰዓት “ከምትገድሉኝ ያለኝን ብትወስዱ ይሻላል” የሚል ሃሳብ በማቅረቡ 17 ብርና የእጅ ሰዓቱን አስረክቦ ሕይወቱን አትርፏል፡፡ በ1970 ዓ.ም የአራት አብዮት ጠባቂዎች መሳሪያ ከተደገነበት በኋላ በስድብና በግልምጫ የተለቀቀበት ታሪክም አለው፡፡
በ1959 ዓ.ም የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪ እያለ፣ በክረምት ወቅት አስመራ ያሉ መምህራንን እንዲያስተምሩ ከተላኩት 10 ያህል አባላት አንዱ የነበረው መስፍን ሀብተማርያም፤ ለግድያ ከተፈላለጉ ሁለት ጓደኞቹ አንደኛው፤ በመሰለኝ ተሳስቶ መስፍን ላይ የተኮሰው ጥይትም ዒላማውን ስቶ ሕይወቱ የተረፈው “አትሙች ያላት ነብስ ቢኖረኝ ነው” ሲል ፅፏል፡፡
ማጠቃለያ
“በምፅፍበት ወቅት የምመርጠው ቦታና ጊዜ የለም፡፡ የግድ ብቸኛ መሆንም የለብኝም፡፡ ጭንቀትና የኑሮ ክርን ካረፈብኝ ግን ቢጨፈልቁኝም ምንም አይወጣኝም” የሚል ምስክርነት በፈርጥ መጽሔት ላይ የሰጠው ደራሲ መስፍን ሀብተማርያም፤ ሥራዎቹ ያስገኙለትን ክብር በሕይወት እያለ ማየት ከታደሉት የጥበብ ሰዎች አንዱ ነው፡፡ 65ኛ የልደት በዓሉን የኢትዮጵያ ሴት ደራሲያን ማህበር በድምቀት አክብረውለታል፡፡ በያዝነው 2006 ዓ.ም መግቢያም የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር የዕውቅናና የምስጋና መድረክ አዘጋጅቶ ደራሲ መስፍን ሀብተማርያምን አወድሷል፡፡ የመጨረሻ ማረፊያውም ታላላቅ ሥራ የሰሩ ኢትዮጵያዊያን ማረፊያ በሆነው በሥላሴ ካቴድራል ሆኗል፡፡

Published in ጥበብ

የቱሪስት መዳረሻ በሆነችው ባህርዳር ከተማ በ43 ሚ. ብር የተገነባው ሆምላንድ ኢንተርናሽናል ሆቴል ዛሬ እንደሚመረቅ የሆቴሉ ባለቤትና ስራ አስኪያጅ አቶ ሙሉጌታ ቢያዝን ለአዲስ አድማስ አስታወቁ፡፡
ሆምላንድ ሆቴል ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ በሶስት ኮከብ ደረጃ አገልግሎት ሲሰጥ መቆየቱን የተናገሩት ባለቤቱ፤ በከፍተኛ ወጪ የማስፋፊያ ስራ እንደተሰራና ወደ አምስት ኮከብ እንዳደገ አስታውቀዋል፡፡ ሆቴሉ 73 ደረጃቸውን የጠበቁ አራት ደረጃ ያላቸው የመኝታ ክፍሎች፣ ከ30-450 ሰዎችን የማስተናገድ አቅም ያላቸው የመሰብሰቢያ አዳራሾች፣ ባርና ሬስቶራንቶች፣ ሰፊ የመኪና ማቆሚያ፣ የሳውና፣ የስቲም ባዝና የማሳጅ አገልግሎቶችን ያሟላ ሲሆን ደረጃውን የጠበቀ የመዋኛ ገንዳውም በቅርቡ ግንባታው ተጠናቆ አገልግሎት እንደሚሰጥ አቶ ሙሉጌታ ተናግረዋል፡፡
ባለአምስት ኮከቡ ሆምላንድ ኢንተርናሽናል ሆቴል፤ ለ153 የአካባቢው ነዋሪዎች የስራ እድል መክፈቱን የተናገሩት ባለቤቱ፤ በኮንፈረንስ ቱሪዝም ቀልብ እየሳበች ላለችው የባህርዳር ከተማ ተጨማሪ ድምቀት እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
ሆቴሉ ዛሬ ረፋድ ላይ የክልልና የፌደራል ባለስልጣናት፣ በቱሪዝም ላይ የተሰማሩ ባለድርሻ አካላት፣ ባለሀብቶችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በድምቀት እንደሚመረቅ ለማወቅ ተችሏል፡፡

          በህገወጥ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና አገልግሎት ላይ ያተኮረ የህዝብ ንቅናቄ መድረክ በደሴ፣ በአላማጣና በሽሬ ከተሞች ባለፈው ግንቦት ወር ተካሂዷል፡፡
የህዝብ ንቅናቄ መድረኩ በተለይ በህገወጥ የምግብና መድሃኒት ንግድ ምንነትና የሚያስከትለው ችግር ላይ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችና ባለድርሻ አካላት ጋር በሰፊው ምክክር ለማድረግና ህብረተሰቡን የቁጥጥሩ ባለቤት ለማድረግ ታልሞ የተካሄደ መድረክ ነው፡፡
የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን፤ ከህገወጥ የምግብና የመድሃኒት ዝውውር ጋር በተያያዘ በጣም ተጋላጭ በሆኑና በተመረጡ ቦታዎች ላይ የህዝብ ንቅናቄ መድረክ ያካሂዳል፣ በቅርቡም በሶስት ከተሞች ላይ የተከናወኑት መድረኮች የዚህ እንቅስቃሴ አካል ናቸው፡፡
በውይይት መድረኮቹ የጤናና ጤና ነክ አገልግሎትና ግብአት ከየት ወዴት፣ ህገወጥ የምግብና የመድሃኒት ንግድና የጤና አገልግሎት ቁጥጥር ነባራዊ ሁኔታ፣ የምግብና የመድሃኒት ህገወጥ ዝውውር አጠቃቀምና ጤና አገልግሎት ክልላዊ ገጽታ፣ ህገወጥ የምግብ፣ የመድሃኒትና ጤና አገልግሎት እንቅስቃሴን በጋራ ለማስወገድ ቀጣይ አቅጣጫ (የጋራ ዕቅድ) የሚሉ ሰነዶች የቀረቡ ሲሆን ለተሳታፊዎች ጥያቄና አስተያየትም በቂ ጊዜ ተሰጥቶ በርካታ ሃሳቦች ተንሸራሽረዋል፡፡
በጋራ ምክክር መድረኩ ትኩረት አግኝተው ከተነሱት ርዕሰ ጉዳዮች አንዱ “ህገወጥ የምግብ፣ መድሃኒት ንግድና የጤና አገልግሎት ቁጥጥር ስራዎች ነባራዊ ሁኔታ” በሚል በባለስልጣን መ/ቤቱ የኢንስፔክሽንና ቅኝት ዳይሬክቶሬት የቀረበው ገለፃ ሲሆን አላማውም በሀገራችን በምግብ፣ በመድኃኒትና በጤና አገልግሎት ዙሪያ ያለውን ህገወጥ እንቅስቃሴ በማስቃኘት በቀጣይ ህገወጥ እንቅስቃሴን በመከላከሉ ስራ ሁሉም የበኩሉን አስተዋጽኦ እንዲያበረክትና ንቁ ተሳትፎ እንዲኖረው ለማነቃቃት ነው፡፡
አግባባዊ የምግብ ንግድ ስራ
ማንኛውም ምግብ ባለስልጣኑ ወይም የክልል ጤና ጤና ተቆጣጣሪ አካል ሳይፈቅድ መመረት፣ ወደ ሀገር ውስጥ መግባት፣ መላክ፣ መዘጋጀት፣ መከማቸት፣ መከፋፈል፣ መጓጓዝ ወይም ለሽያጭ ወይም ለህብረተሰቡ ሊቀርብ አይችልም፡፡
ማንኛውም ምግብ ጥራቱና ደህንነቱ ተጠብቆ መመረት፣ መታሸግ፣ ገላጭ ጽሑፍ መለጠፍ፣ መከማቸት፣ መጓጓዝና መሸጥ አለበት፡፡
በማንኛውም ምግብ ላይ መጠኑን ወይም ክብደቱን ለመጨመር፣ መልኩን ለማሳመር ወይም ለሌላ ተመሳሳይ ዓላማ ሲባል የሰውን ጤና ሊጐዳ ወይም የምግቡን ጥራትና ደህንነት ሊያጓድል የሚችል ባእድ ነገር መጨመር ወይም መቀላቀል የተከለከለ ነው፡፡
ማንኛውም ለህብረተሰቡ ሽያጭ አገልግሎት የሚውል የታሸገ ምግብ በአማርኛ ወይም እንግሊዝኛ ቋንቋ የተፃፈ ገላጭ ጽሑፍ ሊኖረው ይገባል፡፡
የምግቡ ስም
በምግቡ ውስጥ ያለው ይዘት
የምግቡ አምራች ድርጅት ስምና ሙሉ አድራሻ
የምግቡ መለያ ቁጥር (Batch no)
ምግቡ የተመረተበትና የመጠቀሚያ ጊዜው የሚያበቃበት ቀን
አግባባዊ የመድሃኒት ንግድ ስራ
ማንኛውም መድኃኒት ደህንነቱ፣ ፈዋሽነቱና ጥራቱ ተገምግሞ በአስፈጻሚ አካሉ ሳይመዘገብ በጥቅም ላይ ሊውል አይችልም፣
ማንኛውም መድሃኒት ወደ ሀገር ውስጥ ለማስገባት፣ ለማምረትና ለህብረተሰቡ ሽያጭ ለማዋል መጀመሪያ በባለስልጣኑ በብሔራዊ የመድሃኒት መዘርዝር ውስጥ በመካተት ተመዝግቦ የገበያ ፈቃድ ማግኘት አለበት፡፡
የማንኛውም መድሃኒት ገላጭ ጽሑፍ፡-
የመድሃኒቱ ሳይንሳዊ ስም
በመድሃኒቱ ውስጥ ያለው ይዘት
የመድሃኒቱ አምራች ድርጅት ስምና ሙሉ አድራሻ
መድሃኒቱ የተመረተበትና አገልግሎት የሚያበቃበት ጊዜ
በቀን መወሰድ ያለበት መጠንና የአወሳሰድ ሁኔታ…ሊያካትት ይገባል፡፡
አግባባዊ የጤና አገልግሎት አሰጣጥ
ማንኛውም የጤና ተቋም በሀገሪቱ የተቀመጠውን የጤና አገልግሎት ደረጃ ያሟላ መሆን አለበት
ከሚመለከተው የጤና ተቆጣጣሪ አካል ህጋዊ እውቅና የተሰጠው መሆን ይኖርበታል
ለሚሰጠው አገልግሎት የሚያስፈልጉ በቂ የህክምና መሳሪያዎች እንዲሁም ብቃታቸውና ሙያዊ ስነ ምግባራቸው የተረጋገጠ የጤና ባለሙያዎች ሊኖሩት ይገባል፡፡
ባለስልጣን መ/ቤቱ ከላይ ከተገለፀው አግባባዊ አካሄድ በተቃራኒ የሚካሄዱ ህገወጥ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና አገልግሎቶችን ይቆጣጠራል፣ በአዋጅ (661/2002) በተሰጠው ስልጣንና ተግባር መሰረት፣ አስተዳደራዊና ህጋዊ እርምጃም ይወስዳል፡፡ ለአብነት ያህል ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከደንብና አግባብ ውጪ ሲሰሩ በነበሩ ላይ የተጣሉ ቅጣቶችን ማየት ይቻላል፡፡
ወደ ሀገር ውስጥ እንዳይገቡ የተከለከሉ ምርቶች (ባለፉት 9 ወራት)
የምርት ዓይነት         ብዛት በቶን
ምግብ             45 ቶን
መድሃኒት            27 ቶን
ኮስሞቲክስ         14 ቶን
በቁጥጥር ወቅት የተገኙና ተገቢውን መስፈርት ሳያሟሉ ቀርተው የተወገዱ ምርቶች
የምርት ዓይነት         የድርጅቶች ብዛት
ምግብ             127 ድርጅቶች
መድሀኒት             130 ድርጅቶች
አስተዳደራዊ እርምጃ የተወሰደባቸው ድርጅቶች
705 የምግብ አስመጭዎችና ጅምላ አከፋፋይ ድርጅቶች ላይ ቁጥጥር ተካሂዶ 90 ድርጅቶች የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀታቸውን እንዲመልሱ ተደርጓል፡፡ 8 ድርጅቶች ላይ የእገዳ አስተዳደራዊ እርምጃ ተወስዷል፡፡
በ321 መድሃኒት አስመጪና አከፋፋይ ድርጅቶች ላይ ቁጥጥር ተካሂዶ በ24 ድርጅቶች ላይ ከማስጠንቀቂያ ጀምሮ እስከ የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ስረዛ ድረስ አስተዳደራዊ እርምጃ ተወስዷል፡፡
በህዝብ ንቅናቄ መድረኮቹ ላይ የዞንና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮች፣ የክልል ጤና ቢሮ ሃላፊዎች፣ የክልል ተቆጣጣሪ አካላት፣ የፍትህ አካላት (የፍርድ ቤትና ፖሊስ ተወካዮች) የወጣትና ሴት አደረጃጀቶች፣ ከተለያዩ ሴክተር መ/ቤቶች የተውጣጡ ባለሙያዎች (ከገቢዎችና ጉምሩክ፣ ከንግድ ቢሮ፣ ከንግድ አሰራርና ሸማቾች ጥበቃ ባስልጣን….) ተሳታፊዎች ነበሩ፡፡ መሰል የምክክር መድረኮች ችግሮችን በጋራ ነቅሶ ጠቃሚ የመፍትሔ ሃሳቦችን ለመስጠት የሚኖራቸው ፋይዳ ከፍተኛ ነው፡፡ በተለይም በአሁኑ ጊዜ የመላው ማህበረሰብ ችግር የሆነውንና ውስብስብ እየሆነ የመጣውን ህገወጥ የምግብና መድሃኒት ዝውውር ለመግታት፣ የህዝብ ንቅናቄ መድረኮችን ማዘጋጀት የግድ ይላል፡፡ የጤና ጠንቅ የሆነውንና በሁላችንም ህይወት መንገድ ላይ የቆመውን ህገወጥ የምግብና የመድሃኒት ንግድና ዝውውር መግታት የሚቻለው ህብረተሰቡ የቁጥጥሩ ባለቤት መሆን ሲችል ብቻ ነው፡፡ በዚህ ረገድ ባለስልጣን መ/ቤቱ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላትን ብሎም የመላው ማህበረሰብን የተጠናከረ ድጋፍ ይሻል፡፡
ህብረተሰቡ ጥራቱና ደህንነቱ የተጠበቀ ምግብና ጥራቱ፣ ደህንነቱና ፈዋሽነቱ የተረጋገጠ መድሃኒት በመጠቀም ጤናውን ሊጠብቅ ይገባል፡፡ እንዲሁም በምግብ፣ በመድሃኒትና በጤና አገልግሎቶች ላይ ማናቸውም ዓይነት ህገወጥ እንቅስቃሴ ሲገጥመው ለሚመለከተው ተቆጣጣሪ አካልና ለፖሊስ በመጠቆም መተባበር አለበት፡፡
ህገወጥ የምግብና መድሃኒት ንግድና የጤና አገልግሎትን በጋራ እንቆጣጠር!!!
(የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን የህዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ)

Published in ዋናው ጤና

ቤተሰቡ ስለ ጋሻው የተናገረው፡-
ጋሻው የ 26 ዓመት ወጣት ነው፡፡ በቅርቡ ለ 10 ዓመታት ከኖረበት ከ “እንግሊዝ “ አገር  መጥቶ “ደብረዘይት” ወላጆቹ ጋ ይገኛል። እናትና አባቱ ግራ የተጋቡበትን ነገር እንዲህ ሲሉ ለሥነ ልቡና ባለሙያው ገለጹለት፡- “ ልጃችን ብዙ ከቤት አይወጣም፣ ለስራም ሆነ ለሌላ ጉዳይ ወዲያ ወዲህ ለማለት ምንም ፍላጎት የለውም፡፡ ቤተሰቡ ሳሎን ቤት ሲቀመጥ እሱ በጊዜ መኝታ ቤቱ ገብቶ ይተኛል፡፡ ለእራት ሲጠራ ለመብላት  አይፈልግም። እንዳንዴም የግድ ስንለው ምግቡን ቀመስ አድርጎ ወደ መኝታ ቤቱ ገብቶ ይተኛል፡፡ ጠዋትም አምስትና ስድስት ሰዓት ላይ በቅስቀሳ ነው የሚነሳው፡፡ በቃ መተኛት ነው፡፡ ዘመድ መጠየቅ አይፈልግም፤ ጓደኛ እንኳን የለውም፡፡ ስለ ወደፊት ኑሮውም ምንም ደንታ የለውም፡፡ የሚታየውም መልካም ነገር የለም፡፡ የሚገርምህ ተመልሶም ወደ እንግሊዝ አገር ለመሄድ አይፈልግም፡፡ እህቶቹም አልማርና አልሰራ ሲላቸው ነው ወደዚህ የላኩት፡፡ ይኸው ስድስት ወሩ ----ግራ ግብት ብሎናል፡፡”
ጋሻው እና የስነ ልቦና ባለሙያው ተገናኙ፡-
ጋሻው ከስነ ልቦና ባለሙያው ጋር ተገናኝቶ ለካውንስሊንግ ህክምና ፈቃደኛ መሆኑን ስለገለጠለት፣ የስነ ልቦና ባለሙያው በካውንስሊንግ ማዕከሉ “የቅበላ ቃለ መጠይቅ” አደረገለት፡፡ ጋሻው ፈቃደኛ ባይሆንና በቀጣይም ለሚደረገው የካውንስሊንግ አገልግሎት ተባባሪነቱን ባይገልፅ ኖሮ፣ የሥነ ልቦና ባለሙያው በወላጆቹ ፍላጎት ላይ ብቻ ተመስርቶ የሥነ ልቡና ህክምናውን ማድረግ አይችልም፡፡ እናም ጋሻውን እያዘነ ያሰናብተው ነበር። ግን ጋሻው ካውንስሊንግ በህይወቱ ላይ ለውጥ እንደሚያመጣ በ ስነ ልቦና ባለሙያው የተሰጠውን ማብራሪያ ሰምቶ፣ በሂደቱ ውስጥ ለማለፍ ውስኗል-ትክክለኛ ውሳኔ!
ጋሻውን ምን ነክቶት ይሆን? ችግሩስ ምንድነው?
ከላይ ለመግቢያ ያህል የተጠቀምኩበትን መነሻ ሃሳብ በመያዝ  የጋሻውን ችግር ዝርዝሩን እንመልከት፡፡
ድብርት (Depression) ምንድነው?
ድብርት(Depression) ድብርት የተለያየ ደረጃና መጠን ቢኖረውም  በዚህ ፅሁፍ የምናየው ዋናውን ድብርት አምጪ ቀውስ (Major depressive disorder) የተባለውን ነው፡፡
ድብርትን ከመተርጎም መግለፅ ይሻላል፡፡ ድብርት የስሜትና የስነልቦና ችግር ሆኖ ድብርት ያለበት ሰው ስለወደፊት ህይወቱ የሚፈራ፣በአሉታዊ አስተሳሰቦችና እምነቶች የተሸነፈና “ የኔ ህይወት ከእንግዲህ አብቅቶለታል”(my life is over) የሚል እምነት በአብዛኛው የሚታይበት ነው፡፡
እንደ ሥነልቦና ባለሙያዎች ጥናት አንድ ሰው በተከታታይ ቢያንስ ለሁለት ሳምንታት ከደበተው ወይም በማንኛውም ተግባር(activity)ፍላጎትና ደስታ ማጣት ከተጠናወተው፣ ድብርት እንደያዘው ተረድቶ፣ ቶሎ  ወደ ስነ ልቦና ባለሙያ መሄድ ይገባዋል፡፡ በህፃናትና በታዳጊዎች ላይ ከመደበት ይልቅ ንጭንጭ ወይም ብስጭት ጎልቶ ሊታይ ይችላል፡፡
ድብርት የያዘው ሰው ሌሎች ተጨማሪ ምልክቶች ይታይበታል፡፡ እነዚህም ለውጦች የምግብ ፍላጎት መዛባት ወይም የክብደት  ለውጥ፣ የእንቅልፍ መዛባት፣ የስነ አዕምሮ ተግባር መዛባት(psychomotor changes)፣ ሃይል ማጣት፣ የዋጋቢስነት ስሜት ወይም ፀፀት፣ የማሰብ ችግር ወይም ትኩረት ማጣት ወይም ውሳኔ መስጠት ማቃት፣ ተከታታይ የሆነ ራስን የማጥፋት ሃሳብ፣ሙከራ ወይም ዕቅድ መኖር ናቸው፡፡
ከላይ የተጠቀሱት ምልክቶች በአንድ ቀን ውስጥ አብዛኛውን ጊዜና በየዕለቱ በመታየት ለሁለት ተከታታይ ሳምንታት ከዘለቁ ድብርት ውስጥ ተገብቷል ማለት ነው። ድብርት በአንዳንድ ሰዎች ላይ ማህበራዊ ግንኙነታቸውንና የሥራ ሁኔታቸውን ያደናቅፍባቸዋል፡፡ መጠኑ አነስተኛ ከሆነ ደግሞ  ችግሩ ከመከሰቱ በፊት  በቀላሉ የሚሰሩትን ሥራ በብዙ ጥረት ለመስራት ይገደዳሉ፡፡ በድብርት ውስጥ ያሉ ሰዎች ማዘንና ተስፋ መቁረጥ ጎልቶ ይጠናወታቸዋል።
ድብርት በአብዛኞቹ ላይ የምግብ ፍላጎት ማጣትና የክብደት መቀነስ ሲያመጣ፣ በአንዳንዶች ላይ ደግሞ የምግብ ፍላጎት መጨመርና ውፍረትን ያስከትላል፡፡ በልጆች ላይ ሲከሰት ደግሞ እድሜያቸው የሚመጥነውን ክብደት አለማግኘትን ያስከትላል፡፡
ድብርት በአብዛኛው እንቅልፍ ማጣትን የሚፈጥር ሲሆን አንዳንዶች ላይ ግን ከፍተኛና ያልተለመደ የእንቅልፍ ብዛትን ያመጣል ። ሌሊቱ አልበቃ ብሏቸው በቀንም ይተኛሉ፡፡ ጋሻው ከዚህኛው ወገን ይመደባል፡፡ እንቅልፍ ማጣቶች በሶስት ተከፍለው ሊታዩ ይችላሉ፡- ሌሊት እንቅልፍ ማጣት(middle insomnia) ይህ ማለት ሌሊት መንቃትና ተመልሶ መተኛት አለመቻል፣ በመጨረሻ ላይ እንቅልፍ ማጣት (terminal insomnia) ይህም በጣም ቶሎ መንቃትና ተመልሶ መተኛት አለመቻል፣ ከጅምሩ እንቅልፍ ለማግኘት መቸገር( initial insomnia) ተብለው ይመደባሉ።
ድብርት የአእምሮ ለውጦችም (psychomotor changes) ሊፈጥር ይችላል። ለምሳሌ አንድ ቦታ ቁጭ ማለት አለመቻል፣እጅን መጭመቅ፣ ቆዳን መጎተት ወይም ቆዳን፣ልብስን ወይም ሌላን ነገር ማሸት እንዲሁም ንግግር መቀነስ ወይም ድምፅን ዝቅ አድርጎ መናገር፣ ምላሽ ከመስጠት በፊት ለመናገር ጊዜ መውሰድ ሊፈጥር ይችላል።
ሃይል ማጣትና ከፍተኛ ድካምም በአብዛኛው የድብርት መገለጫዎቹ ናቸው፡፡
ጠቅለል አድርገን ስናየው ለድብርት (Major Depressive Episode) የሚከተሉት መለያ ምልክቶች እንደሚታዩ  የስነ ልቦና ምሁራን ይስማሙባቸዋል፡-
 በየዕለቱ አብዛኛውን የቀኑን ውሎ መደበት፣ ይህም ድብርት የያዘው ሰው ማዘኑንና ባዶነት እንደተሰማው በገፅታው ወይም በሌላ ሰው ግንዛቤ ለምሳሌ ሲያለቅስ በመመልከት መገንዘብ ይቻላል። በልጆችና በታዳጊዎች ላይ ብስጭት ይታያል።
በአብዛኛው ወይም በሁሉም ነገር የተጋነነ  ፍላጎት ወይም ደስታ ማጣት፡፡ ይህም አብዛኛውን የዕለት ኑሮና በአብዛኛው በየዕለቱ ሲሆን ይህም በሚገልፀው ወይም በምልከታ የሚረጋገጥ ነው።
የምግብ ፍላጎት ለሚያጣ የሚፈጠር ከፍተኛ ክብደት መቀነስ ወይም የምግብ ፍላጎቱ ለሚጨምር ከፍተኛ ክብደት መጨመር። በሁለቱም አቅጣጫ በየወሩ (ከአምስት በመቶ በላይ ለውጥ መገንዘብ። በህፃናት ዘንድ በእድሜያቸው ማግኘት የሚገባቸውን ክብደት አለማግኘት ጠቋሚ ነው።
በአብዛኛው በየዕለቱ እንቅፍ ማጣት ወይም እንቅልፍ መጨመር
በአብዛኛው በየዕለቱ የሚከሰት አዕምሯዊ ቸግር (psychomotor agitation or retardation):- በሌሎች እይታ ውስጥ የሚገባ መናወጥ
በአብዛኛው በየዕለቱ የሚገለፅ ድካምና ኃይል ማጣት
በአብዛኛው በየዕለቱ የሚሰማ የዋጋ ቢስነት ስሜት ወይም አግባብ ያልሆነ ራስን የመኮነን ስሜት(guilt)
በአብዛኛው በየዕለቱ የማሰብ አቅምን ወይም ትኩረት ማድረግን ማጣት፣መወሰን አለመቻል። ይህም ድብርት በያዘው ሰው ገለፃ ወይም በምልከታ ሊረጋገጥ ይችላል።
ተከታታይ የሆነ ራስን የማጥፋት ሃሳብ (የሞት ፍርሃትን አይመለከትም)፡፡ ይህም ራስን የማጥፋት እቅድ ሳይኖር የ ሃሳቡ በአዕምሮ ውስጥ መመላለስ ወይም ራስን የማጥፋት ሙከራ ማድረግ ወይም ራስን ለማጥፋት ዕቅድ አውጥቶ መመላለስ ሊሆን ይችላል።
ድብርት ከየት ይመጣል?
በሳይኮ አናሊቲክ ዘርፍ ያሉ ምሁራን፤ ልጆች  በለጋ እድሜ  ከፍተኛ ቅርርብ ከፈጠሩት ሰው (እናት፣አባት ወይም አሳዳጊ ሊሆን ይችላል) ድንገት መለየታቸው ከሚያመጣው ከባድ ስነ ልቦናዊ ችግር፣  በአዋቂነት ዘመናቸው ከሚወዱት ሰው መለየትና ጥቂት ፍቅር ማጣት ወይም መነፈግ  ተጋላጭ ሊያደርጋቸውና ለድብርት ሊዳርጋቸው ይችላል ብለው ትንታኔ ይሰጣሉ፡፡
“ራስን አለመርዳት ተሞክሮ” (learned helplessness) ማለትም ከዚህ በፊት የገጠመንና በድል ያልተሻገርነው እንቅፋት ሲኖር ወደፊትም አልሻገረውም የማለት አስተሳሰብና ተስፋ መቁረጥ በምክንያትነት የሚጠቀስበትም ሁኔታ አለ፡፡ አንድ ሳይኮሎጂስት( ከርት ሪቸር-Curt Ritchter ይባላል) በሁለት አይጦች ላይ አንድ ጥናት አካሄደ፡፡ አንዷን አይጥ በእጁ ያዘና ሞቅ ወዳለ  ውሃ የተሞላ ባልዲ ውስጥ ከተታት፡፡
አይጧ ለ 60 ሰዓታት ያህል ተስፋ ሳትቆርጥ  ተንፈራግጣ በመጨረሻ አቃታትና ሰመጠች፡፡ ሁለተኛዋን አይጥ ደግሞ እጁ ላይ ለረዥም ጊዜ እንድትፈራገጥ አደረገና ማምለጥ እንደማትችል ስታረጋግጥና እንቅስቃሴዋን ስታቆም፣ ወደ ባልዲው ከተታት፡፡ አይጧ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ ውሃ ውስጥ ሰመጠች፡፡ የሳይኮሎጂስቱ ትንታኔ፤ የሁለተኛዋ  አይጥ በተወሰነ ደረጃ ውሃ ውስጥ ከገባች በኋላ መንፈራገጥ ነበረባት ነገር ግን የበፊቱ በእጅ ላይ በቆየችበት ተሞክሮዏ ማምለጥ እንደማትችል ተምራለች በዚህም ምክኒያት ለገጠማት ሁለተኛው እንቅፋት(challenge) ተስፋ ቆርጣለች፡፡ ከዚህ ተሞክሮ በኋላ  ሳይኮሎጂስቶች ጉዳዩን እየመረመሩት በመምጣት ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ  “ ራስን አለመርዳት ተሞክሮ ሞትን፣ለውጥንና በህይወት የሚያጋጥም ጫናን ለመቋቋም ያለ ፍላጎትንና ችሎታን እንደሚያዳክም በመግለፅ የድብርት አንዱ ክፍል ለመሆን በቅቷል” ይላሉ፡፡
በሌላ በኩል ቤክ (Beck) የተባለ ሳይኮሎጂስት፤ ዋናው የድብርት መገለጫ ባህሪ አሉታዊ የሆነ ግምት(expectaion) እና አስተሳሰብ መሆኑን በማብራራት፣ ይህም ድብርት የያዘው ሰው ዋና መገለጫ ነው ብሎ ያምናል፡፡ ይህ ሰው ድብርትን ከአሉታዊ አስተሳሰብ ጋር ያቆራኘዋል፡፡ በዚህም መሰረት ሶስት ገፅታ ያላቸው ከአስተሳሰብ ጋር የተገናኙ አሉታዊ አስተሳሰቦች የድብርት መገለጫዎች ናቸው ይላል፡፡
የመጀመሪያው ገፅታ ስለ ራስ ያለ አሉታዊ ግምት ነው፡፡ ሁለተኛው ገፅታ፣ የራስ ተሞክሮን በአሉታዊ መልኩ ትንታኔ መስጠት ነው፡፡ ይህም ማለት የተሰሩ ስራዎችን፣የተሞከሩ ድርጊቶችና ግንኙነቶችን በአሉታዊ መልኩ ትንታኔ በመስጠት ራስን መኮነን ነው፡፡ ሶስተኛው ገፅታ፤ ስለ ወደፊት(future) አሉታዊ አስተሳሰብ ማሰብ ነው ይላል። በዚህ ምሁር አረዳድ፣ ድብርት ከላይ የተገለፁትን አስተሳሰቦች ከማምጣት አቅሙ በላይ  እነዚህ አስተሳሰቦች የሰውን ስሜት የመጫን ወይም ድብርትን የመፍጠር አቅማቸው ከፍተኛ ነው ብሎ ያምናል፡፡ በአብዛኛው የድብርት ሰለባ የሆኑ ሰዎች ተገቢ አስተሳሰብ ባይሆንም በህይወታቸው ለገጠማቸው አሉታዊ ተሞክሮ ራሳቸውን ተጠያቂ በማድረግ፣ አሉታዊ ተሞክሮዎቹ ጥፋቶቻቸው እንደሆኑ አድርገው ይወስዳሉ፡፡
ሌሎች ደግሞ በአንጎል ውስጥ ያለ የኬሚካሎች መጠን መዛባት ለድብርት መነሻ ነው ብለው ይገምታሉ፡፡ ይህንንም ሲያስረዱ፤ ለ ድብርት የሚሰጡትን መድሃኒቶች ተፅእኖ በመመልከት ግምታቸውን ያስቀምጣሉ፡፡ ለምሳሌ ሜ ኤ ኦ አጨናጋፊ (MAO Inhibitors) የተባለው ለድብርት የሚሰጠው መድሃኒት ኖርኢፒንፍሪን (norepinephrine) የተባለውን በአንጎል ውስጥ የሚገኝ ንጥረ ነገር የማቆየት ሃይል እንዳለውና የዚህ ንጥረ ነገር  በአንጎል ውስጥ መቀነስ ከድብርት ጋር ይገናኛል የሚል ግምታቸውን ያስቀምጣሉ።
በሌላ መልኩ ደግሞ ሌሎች ሳይኮሎጂስቶች የድብርት ጉዳይ ከሌሎች ጋር ባለ ግንኙነት ሊታይና ሊተነተን ይገባል ይላሉ፡፡ ኮይኔ(Coyne) የተባሉ ተመራማሪ፤ ሰዎች ከሌሎች ሰዎች ጋርና ከአካባቢያቸው ጋር ያላቸው ግንኙነት እንደዋዛ የሚታለፍ አለመሆኑን ጠበቅ አድርገው ይናገራሉ፡፡ ከዚህም ጋር አያይዘው የድብርት ሰለባ የሆኑት ሰዎች ተግባራዊ እንቅስቃሴ የሚገደበው ጤናማዎቹ ሰዎች ከእነሱ ጊዜ ለማሳለፍ ፈቃደኛ አለመሆናቸው ያመጣባቸው  ችግር ነው ባይ ናቸው፡፡
ጋሻውና መድሃኒቱ፡
ህክምናውን በሶስት ከፍለን ብናየው፡-
በራሱ በግለሰቡ የሚደረግ
በርታ ብሎ ትናንሽ ግቦችን በማስቀመጥ፣ በየዕለቱ አንድ ነገር ለመስራት መሞከር፡- ለምሳሌ  ብዙ ለሚተኙ የስምንት ሰዓት እንቅልፍ እንደ ግብ ማስቀመጥና ተፈፃሚ ለማድረግ መሞከር፤
ከሚወዱትና ከሚያምኑት ሰው ጋር ጊዜ ወስዶ ችግርን መግለፅና የሚፈልገውን እገዛ እንዲያደርጉለት መጠየቅ፤
ምንም እንኳን ፍላጎት ቢጠፋም ጨክኖ ማህበራዊ እንቅስቃሴዎች ውስጥ ለመግባት መሞከርና ከሰዎች ጋር መቀላቀል፤ በተለይም መልካም ነገር ከሚናገሩና ተስፋ ካላቸው ሰዎች ጋር ማሳለፍ፤
አሉታዊ አስተሳሰቦችን መቋቋም -ለራስ ርህራሄን በመስጠት ራስን ተጠያቂ ማድረግንና መኮነንን ጋብ ማድረግ፤
የፍፁምነትን አስተሳሰብ መጨቆን- ብዙ ጊዜ ስህተትንና ደካማ ጎንን አለመቀበል፣ በድብርት ተጠቂዎች ዘንድ ስለሚታይ፣ ሰው ሁሉ ፍፁም እንዳልሆነ በመረዳት አስተሳሰቡን ለመጨቆን መሞከርና “ሁልጊዜ፤ በፍፁም፤ሁሉም፤” ወዘተ የሚሉ ቃላት ማስወገድ፡፡
በግል የተደረገው ጥረት መፍትሄ ካላመጣ የሚከተሉትን ሁለት አማራጮች መጠቀም አስፈላጊ ነው፡፡
በስነ ልቦና ባለሙያ(ካውንስለር) የሚደረግ ድጋፍ፡-
በስነልቦና ህክምና ድብርት የያዘው ሰው መድሃኒት ላለመጠቀም ነፃ የሚሆንበት ዕድል አለ፡፡ ካውንስለሩ ድብርት ከያዘው ሰው ጋር በሚያሳልፍበት ጊዜ የባህሪና የስሜት ህክምና ቴክኒኮችን በመጠቀም ከችግሩ ነፃ የሚሆንበት መንገድ ይከተላል፡፡ በሂደቱ ችግር የገጠመው ሰው የሚተገብራቸው በርካታ ተግባራት ከስነ ልቦና ባለሙያው ስለሚሰጡት  የግለሰቡ መሉ ፈቃደኝነት ወሳኝ ሚና ይጫወታል፡፡
የሳይካትሪስት ድጋፍ፡-
የስነልቦና ባለሙያው ከጋሻው ጋር ባሳለፈው የተወሰኑ ጊዜያቶች የተረዳው ነገር ነበር፡፡ ጋሻው ከፍተኛ የሆነ ራስን የማጥፋት ሃሳብ ነበረው፡፡ በመሆኑም በስነልቦና ባለሙያው ውሳኔ ጋሻው ወደ ሳይካትሪስት ሄዶ “ማስታገሻ” መድሃኒት መውሰድ እንዳለበትና ለዘለቄታ መፍትሄው ግን በካውንስሊንግ የሚገኘውን ህክምና ጎን ለጎን ክትትል በማድረግ፣ ከድብርቱ እንዲወጣ ማሳሰብ ነበር፡፡ ጋሻውም ያደረገው ይህንኑ ነው፡፡
የስነ ልቦና ባለሙያው በስነልቦና ክትትል ብዙ ለውጥ ማምጣት የማይቻልበት ደረጃ መሆኑን ካረጋገጠ፣ የድብርት ተጠቂውን ሰው በሳይካትሪስት እንዲታይ ይልከውና መድሃኒት እንዲወስድ፣ ቀስ በቀስ ደግሞ መድሃኒቱን በመቀነስ በ ካውንስሊንግ አገልግሎት ጤናውን እንዲጎናፀፍ ያበረታታዋል፡፡
 አንዳንዴ ለመጠነኛ ድብርትና ጭንቀት ሆስፒታል ለሚሄዱ ሰዎች፣ ሳይካትሪስቶች ፈጥነው መድሃኒት ሊሰጧቸው አይገባም፡፡ ይልቁንም መደረግ ያለበት ወደ ስነ ልቦና ባለሙያ እንዲመሩና (Refer እንዲደረጉ)  የስነልቦና ህክምና ክትትል በማድረግ ጤናቸውን እንዲጎናፀፉ መጣር ነው፡፡
ውድ አንባቢያን፡- ከላይ የተጠቀሰውን ጋሻውን አታገኙትም-----የለምና!---- ለማስተማሪያ ታስቦ እዚሁ ወረቀት ላይ የተጀመረና ያለቀ ገጸባህሪ ነው፡፡
ቸር እንሰንብት
(ፀሐፊውን በተከታዩ ኢ-ሜይል፡ This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.
ማግኘት ይችላል)

Published in ዋናው ጤና

“መስፍን ቅንና
ግልፅ ሰው መሆኑን አውቃለሁ”
(ደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕል)
መስፍን ሀብተማርያም በሁለት በኩል አስተዋፅኦ አበርክቷል፡፡ አንደኛው ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በወግ ስነ-ፅሁፍ ዘውግና በሌላውም ዘርፍ ከ10 ዓመት በላይ አስተምሯል፡፡ መስፍን ራሱ ከሚፅፈው ውጭ የሚፅፉ የፈጠራ ሰዎችን በመፍጠር ከፍተኛ ድርሻ ነበረው፡፡ ውጭ አገር በወግ አፃፃፍ፣ በአጫጭር ልቦለድና በሌሎች ስነፅሁፎች ላይ ትምህርቱን ተከታትሎ ከመጣ በኋላ፣ የተማረውን ወደ ተማሪዎች በማስተላለፍ ብዙ ፀሐፍትን አፍርቷል፡፡ ይሄ የመጀመሪያውና ትልቁ አገራዊ አስተዋፅኦ ነው፡፡
ሁለተኛው ከዩኒቨርሲቲ ከወጣ በኋላ ኩራዝ አሳታሚ ድርጅት ውስጥ በሰራበት ወቅት ያበረከተው አስተዋፅኦ ነው፡፡ በዚያን ወቅት ቦርዱ ያሳለፋቸውን መፅሀፍት (የቦርድ አባል ይሁን አይሁን አላስታውስም) ይህን አሟላ፣ “ይህን ቀንስ፣ ይህን አዳብር” እያለ መፅሀፍት ለአንባቢው እንዲመጥኑ ሆነው እንዲወጡ በማድረግ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበርክቷል፡፡ አርታኢ፣ ገምጋሚና ሀያሲ ሆኖ ሰርቷል፡፡ ፅሁፎቹም የአገር ሀብትና አስተማሪ ናቸው፡፡
ስብዕናውን በተመለከተ በቅርበት ባላውቀውም ግልፅና ቅን ሰው መሆኑን በተለያዩ የስራ አጋጣሚዎች በተገናኘን ጊዜ ለመረዳት ችያለሁ፡፡ በመፅሀፍት ምረቃ፣ በስነ ፅሁፍ ውይይቶች እና መሰል ዝግጅቶች ላይ ተጋብዞ ሲመጣ፤ ለግማሽ ቀን፣ ለሙሉ ቀን አሊያም ለሁለት እና ሶስት ሰዓታት ስንገናኝ ቅንነቱ ጎልቶ ይታያል። የሚጠየቀውንም ጥያቄ አቅሙ እስከፈቀደ ድረስ ለመመለስ ጥረት ሲያደርግ እመለከታለሁ። በተለያዩ መፅሄቶች በርካታ ፅሁፎቹን ሳነብ በጣም ያዝናናኝ ነበር፡፡ ይህን መሰል ትልቅ ሰው ማጣት ጉዳት ነው። አንድ መፅሄት ላይ የመስፍን ፅሁፍ ካለ፣ መፅሄቱን ገዝቼ መጀመሪያ የማነበው የእሱን ጽሁፍ ነው፡፡ ለምን? ሳያስጨንቅሽ ነው ህይወትን በፅሁፍ የሚያሳይሽ፡፡ ሌላው በ1970ዎቹ ከጋዜጠኛ ታደሰ ሙሉነህና ከነመዓዛ ብሩ ጋር የእሁድ ፕሮግራም ሬዲዮ ዝግጅት ላይ ሲካፈል በነበረበት ጊዜ፣ በጣም በጣም ተወዳጅ ነበር፡፡ መስፍንን ይህን ያህል ነው የማውቀው፡፡
“በህዝቡ ውስጥ ኖሮ ያለፈ
ሰው ነው”
(ደራሲና ጋዜጠኛ ዘነበ ወላ)
በኢትዮጵያ ስነ-ፅሁፍ የመጀመሪያውን የወግ አፃፃፍ መንገድ ከዘረጉት ውስጥ የሚመደብ ነው። እንደሚታወቀው ደበበ ሰይፉ ለመስፍን “የቡና ቤት ስዕሎች” ላይ ግሩም የሆነ መግቢያ ፅፎለታል፡፡ የዝቅተኛውን ማህበረሰብ ህይወትም እንድናስተውል ያደረገን ጋሽ መስፍን ነው፡፡ ይህንን ስትመለከቺ ድንቅ ጸሐፊ ነው ከማለት ውጭ ምን ትያለሽ፡፡ ስብዕናውን ስትመለከቺ “Simple person” የምትይው አይነት ሰው ነው፤ ጋሽ መስፍን፡፡ የማይከብድ፣ ከቀረብሽው ሰዓት ጀምሮ እንደራስሽ አካል የምታይውና የሚገርም ሰው ነው፡፡ አቅሙ በፈቀደው መጠንም ሰዎችን ለመርዳት ሙከራዎችን ሲያደርግ ማየቴን አስታውሳለሁ፡፡ ወጣት ደራሲያንን በመፍጠር በኩል ያደረገው አስተዋፅኦ በቃላት የሚገለፅ አይደለም፡፡ እኔና ጋሽ መስፍን የዛሬ 26 ዓመት አስመራ ከተማ መሀል አራዳ ላይ ተገናኝነተን ነበር፡፡ በወቅቱ እኔ መርከበኛ ስለነበርኩኝ ዳህካክ ቀይ ባህር ላይ ነበር የምሰራው፡፡ ለአጭር ኮርስ አስመራ ወጥቼ ነው ያገኘሁት፡፡ እኔ አውቀው ስለነበር ሰላምታ ሰጥቼ ራሴን አስተዋወቅሁት፡፡ ከዚያም “ስነ-ፅሁፍ እንድታስተምረኝ እፈልጋለሁ” አልኩት፡፡ “አንተ ደግሞ ስለባህር ታስተምረኛለህ” አለኝ፡፡ እኔ ግን ደነገጥኩ፤ ምክንያቱም ደራሲ ሀያሲ ሲባል ሁሉንም የሚያውቅ ነበር የሚመስለኝ፡፡ “እንዴት እንደዚህ ትለኛለህ?” ጋሽ መስፍን?” አልኩት፡፡ “እኔ የስነ-ፅሁፍ ኤክስፐርት ነኝ አስተምርሃለሁ፤ አንተ ስለ ባህር ታውቃለህ ታስተምረኛለህ” አለኝ ደጋግሞ፡፡ ቀጠለናም “በአለም ላይ ስንት የባህር ስነ-ፍጥረታት አሉ?” ሲል ጠየቀኝ። “ወደ 30 ሺህ የሚጠጉ በባህርና በውቅያኖስ የሚኖሩ ስነ ፍጥረታት አሉ” አልኩት፡፡ “ዘነበ፤ ይሄ በቁጥር ስታገኘው ቀላል ሊመስልህ ይችላል፤ ግን አንተ ስትፅፍ ምርጥ ምርጡ ላይ አተኩር” አለኝ፡፡ የዚያን ጊዜ አንጎሌ ውስጥ ያለውን ሼል እንክት አድርጎ ሰበረው፡፡ የሰው ልጅ እድሜ አጭር ነው፤ ሊያውቅ የሚችለውም ውስን ነገር ነው፤ ጎበዞቹና የተቀቡት ግን ቶሎ ቶሎ ሰርተው አልፈዋል፡፡ ለምሳሌ ሼክስፒርን ውሰጂ፤ እዚህ ምድር ላይ የቆየው 52 ዓመት ብቻ ነው፤ ስራዎቹ ግን እስካሁን አሉ፤ ወደፊትም ይኖራሉ፡፡ ጋሽ መስፍን እኔን የመራኝ ወደዚህ ነው፤ ምርጥ ምርጦቹ ላይ አተኩር በማለት፡፡ ሁሌም አንድ ነገር ሳስብ ይህቺ አባባሉ የእኔ መነፅር ናት። ስለ 30 ሺህ ስነ-ፍጥረታት ባለፉት 26 ዓመታት ባነብ እንኳን አልጨርስም፤ በምርጥ ምርጡ ላይ አተኩሬ ግን “ህይወት በባህር ውስጥ” የምትል አንድ መፅሀፍ ለመፃፍ በቅቻለሁ፡፡ መፅሀፉን ያዘጋጀሁት ትንሹን የእጅሽን ጣት ከምታክለው አሳ እስከ አሳ ነባሪ ድረስ ያለውን የአሳ ዝርያ አጥንቼ ነው፡፡ በማዘግምበትና በማስብበት ጊዜ ሁሉ “ከምርጥ ምርጡ ላይ አተኩር”  የሚለው የጋሽ መስፍን ምክር አብሮኝ አለ፡፡ ጋሽ መስፍን መደበኛ ባልሆነ መልኩ አስተምሮኛል ማለት እችላለሁ፡፡ በህይወቱም ቀለል ብሎ ከማህበረሰቡ ጋር ተቀላቅሎ ነበር የሚኖረው፡፡ የደራሲ ህይወት ደግሞ ይሄ ነው፡፡
በአንድ ወቅት ጋሽ ስብሀትን “አንዲት ቮልስ ስዋገን ብትኖርህ ኖሮ መጭ ትላትና የፈለግህበት ታደርስህ ነበር” አልኩት፡፡ “ኖ! ማሽን ከህዝብ ይነጥልሀል፡፡ በህዝብ ውስጥ የምትኖር ከሆነ የቴክኖሎጂ ውጤቶችንና ማሽኖችን መጠቀም የለብህም” ብሎኛል፡፡ ጋሽ መስፍንም ቢሆን በህዝብ ውስጥ እየኖረ ያለፈ ሰው ነው፡፡
“የአማርኛ ወግ የተጀመረውም ፈር የያዘውም በጋሽ መስፍን ነው”
(ደራሲና ሃያሲ አለማየሁ ገላጋይ)
ጋሽ መስፍን ሃብተማርያም በኢትዮጵያ ስነ-ፅሁፍ ውስጥ ትልቅ ቦታ ያለው ሰው ነው፡፡ የአማርኛ ወግም የተጀመረው በእሱ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ የተጀመረው ብቻ ሳይሆን ፈር የያዘውም በመስፍን ሃብተማርያም ነው፡፡ በ1970ዎቹ መጀመሪያ ላይ ሲፅፋቸው የነበሩት ወጎች፣ በአንድ ላይ ተሰብስበው ለኩራዝ አሳታሚ ድርጅት ሲሰጡ ምን ተብሎ መሰየም እንዳለበት ግራ መጋባት ፈጥሮ ነበር፡፡ ምክንያቱም ያን ጊዜ ወግ በአማርኛ ስነ-ፅሁፍ ውስጥ አልነበረም፡፡ ስለዚህ ጋሽ አስፋው ዳምጤና ደበበ ሰይፉን በማስጠራት “እስኪ ምን ብለን እንሰይመው? ምከሩን” የሚል ጥያቄ አቀረበ፡፡ ከዚያም እነሱ ተነጋግረው “ድርሰት” ብለውት ነበር፡፡ በኋላ ግን ደበበ ሰይፉ ወግ ቢባል ይሻላል አለ፡፡ ወግ የሚባለው የስነ-ፅሁፍ ዘውግ የደረሰን በጋሽ መስፍን ነው፡፡ እሱ የሳይንሳዊ እውቀቱም አለው፤ ተሰጥኦውም አለው፡፡ ይሄንንም ከ250 በላይ ወጎችን በመፃፍ አሳይቷል፡፡ ጋሽ መስፍን ወግ መጀመር ብቻ ሳይሆን ተስፋፍቶ በወጣት ደራስያን እንዲቀጥል አድርጓል፡፡ በኢትዮጵያ ሬዲዮ ጭምር ወጎቹን በመተረክ ህብረተሰቡ ለወግ ቅርበት እንዲኖረው ማድረግ ችሏል፡፡ በእነ በዕውቀቱ ስዩም፣ በእነ በሃይሉ ገ/እግዚአብሔር፣ በእነ ኤፍሬም ስዩም.. የታየው ወግ፣ ያኔ በጋሽ መስፍን ተፅዕኖ የመጣ ነው። በእንግሊዝ እነ ፍራንሲስ ቤከን የወግ ጀማሪ የሆኑትን ያህል በአማርኛም የወግ ጀማሪው ጋሽ መስፍን ነው። እነፍራንሲስ ቤከን በአገራቸው እንደጀማሪነታቸው ያገኙትን ክብር ጋሽ መስፍንም ሊያገኝ ይገባል ባይ ነኝ፡፡ እንግዲህ በአማርኛ ስነ-ፅሁፍ ውስጥ ያለው ቅሬታ አንጋፋ ደራሲዎች ወጣቶቹን ለማቅረብ ሰፊ ሆድ የላቸውም የሚል ነው፡፡ እንደውም ደራሲ አዳም ረታ “እንደ ጠርሙስ ልሙጥ ናቸው፤ ወጣቱን ለመሸከም የሚችል ትከሻ የላቸውም” ይላል፡፡ ይህ አባባል በጣም ትክክል ነው፡፡ ጋሽ መስፍን ሃ/ማርያም፣ አስፋው ዳምጤ፣ ስብሃት ገ/እግዚያብሔርና አብደላ እዝራ ጋር ስትሄጂ ግን ትከሻ ያላቸው ሰዎች ናቸው፡፡
እኔ ጋሽ መስፍንን በሁለት የህይወቴ ጫፍ ሁለት ጊዜ አግኝቼዋለሁ፡፡ በመጀመሪያ ስነ-ፅሁፍ ምን ማለት እንደሆነ እንኳን በወጉ ሳይገባኝ፣ ምንም በነበርኩበት ጊዜ አግኝቼው ያናገረኝ በከፍተኛ ትህትናና ፍቅር ነው። ስለ ስነ-ፅሁፉም ቢሆን ሲያበረታታኝ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ የእኔን ፅሁፎች አንብቦ ሂስ ከሰራ በኋላ ሰያገኘኝም የመጀመሪያው ዓይነት አክብሮትና ትህትና ነው ያሳየኝ። ምንም ነገር ሳትይዥና የሆነ ነገር ይዘሽ ስትቀርቢ አቀራረቡ መለያየት ነበረበት፡፡ ለማንም ቢሆን ጥሩ ወዳጅ ነበር፡፡ ጋሽ መስፍን ለወጣቶቹ እንደመሸሸጊያ ጥላ ነበር፡፡ በሥነ-ፅሁፍ ሰፊና መሸሸጊያ የሆነን ሰው ማጣት ለስነ-ፅሁፉም የራሱ የሆነ ትልቅ ጉዳት አለው፡፡ ይህ ጉዳት በተተኪዎቹ ላይ ተፅዕኖ በመፍጠር ነው የሚታየው፡፡ ዞሮ ዞሮ የጋሽ መስፍን መልካም ባህሪ ስነ-ፅሁፉን አግዞታል የሚል እምነት ነው ያለኝ፡፡
“በወግ ፀሀፊያን ዘንድ የመስፍን አሻራ ጎልቶ ይታያል”
(ደራሲና ጋዜጠኛ በሃይሉ ገ/እግዚአብሔር)
ስለአጠቃላይ የወግ ፅሁፍ ሲነሳ፣ በጉልህ የሚነሳው መስፍን ሃብተማርያም ነው፡፡ አሁን ወግ በሚፅፉ ፀሃፊያን ላይ የመስፍን አሻራ ጎልቶ ይታያል፡፡ ለምን ቢባል በሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት እያለን የተማርነው በመስፍን ሃ/ማርያም መፅሀፎች ነው፡፡ በኮሌጅ ደረጃም ስነ-ፅሁፍን ስንማር የእሱ ስራዎች ናቸው ተጠቃሾቹ፡፡ እስከዛሬ ድረስ በወግ አፃፃፍ ዘውግ ውስጥ በቀዳሚነት የሚጠቀሰው መስፍን ሃብተማርያም ነው፡፡ እነ “አውድአመት”፣ “የቡና ቤት ስዕሎች” የመሳሰሉት ስራዎቹ የሚዘነጉ አይደሉም፡፡
እነዚህ ስራዎች ከእሱ በኋላ ለመጡትም ሆነ አሁን ላሉት የወግ ፀሐፊዎች ፈር ቀዳጅ ናቸው። አሁን የወግ መፅሀፍ ፅፈው ለሚያሳትሙትም ሆነ በየጋዜጣው ላይ በአምደኝነት ለሚፅፉት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የመስፍን እጅ አለበት፡፡ የወግ ጸሀፊያን እየበዙ መምጣታቸው በራሱ፣ ጋሽ መስፍን በስነ-ፅሁፉ ውስጥ ያለውን ጉልህ ድርሻ የሚያሳይ ነው፡፡ እኔ በጣም ቀርቤው ባላውቅም በሌሎች ወጣት ደራሲያን በኩል ስሰማ፣ በጣም አጋዥና በተቻለው አቅም ሁሉ ገንቢ አስተያየቶችን የሚሰጥ መሆኑን ነው የምረዳው። እኔ እንደውም ሃያሲ ሲባል ጋሽ መስፍን ወጣቶችን ለማበረታታት የሚሰጣቸው አስተያየቶች ናቸው የሚታሰቡኝ፡፡ ስብዕናውን በተመለከተ የጠለቀ ቅርርብ ስለሌለን ብዙ ማለት አልችልም፡፡ ከስራዎቹ ጋር ነው የበለጠ ትውውቅ ያለኝ፡፡ ለረጅም ጊዜ በመጽሔቶች ላይ በሚፅፋቸው ፅሁፎችና ባሳተማቸው መፅሃፍቱ በደንብ አውቀዋለሁ፡፡ ህልፈቱ ለስነ-ፅሁፍ በጣም ጉዳት ነው፡፡
“መስፍን አንጀት አርስ ደራሲ ነው”
(ጋዜጠኛ እሸቴ በቀለ)
እርግጥ መስፍን ሃ/ማርያም በዩኒቨርሲቲ ደረጃ እኔን በቀጥታ አላስተማረኝም፡፡ እኔ ወደ ዩኒቨርሲቲ ስገባ እሱ ወጥቶ ነበር፡፡ ነገር ግን ከጋሽ መስፍን ጋር በስነ-ፅሁፍ ስራ እንገናኝ ነበር፡፡ አንድ መስሪያ ቤትም ሰርተናል። በአጠቃላይ ግን መስፍን አንጀት አርስ ደራሲ ነው እላለሁ፡፡ ጋሽ መስፍን የሚፅፋቸውን ወጎች ስታነቢ ስዕል ከስቶ ነው የሚያመጣልሽ፡፡ “ወግ እንደዚህ ይፃፋል ወይ?” እንድትይ ያደርግሻል፡፡ እኔ ወግ ፀሀፊ ጥራ ብትይኝ አንድና አንድ መስፍን ሃብተማርያም ነው፡፡ በተለይ “የቡና ቤት ስእሎች”ን ያነበብኩ ጊዜ ወግ እንዲህም አለ ወይ ነው ያስባለኝ፡፡ ስለ አጭር ልብወለድ ስናወራ ብዙ የተፃፈ ነገር አለ፡፡ “Essay” የሚለውን ነገር በተመለከተ ግን እንዲህ ንጥር ባለ መልኩ ሊፃፍ እንደሚችል ያሳየ ብርቱ ሰው ጋሽ መስፍን ነው፡፡
ከዚያ በኋላም ብዙ ፅሁፎችን በየመፅሄቱ ፅፏል፡፡ በስብእና ደረጃም ቢሆን ጋሽ መስፍን በምንም መልኩ ሰውን የሚያስቀይም አልነበረም፡፡ ጋሽ መስፍን አጠገብሽ ከተቀመጠ አንቺ ያለብሽ መሳቅ ብቻ ነው፡፡ ድንጋይን የማሳቅ ሁሉ ኃይል ያለው ይመስለኛል፡፡ ሲያስቅሽ ደግሞ ተራ የወረደና ትንንሽ ጆክ አይደለም የሚያወራሽ፡፡ ከትምህርቱ፣ ከእውቀቱ ጋር የሚመጣጠን ቁም ነገር አዘል ቀልድ ነው የሚናገረው፡፡ ለምሳሌ አብረሽው ሆነሽ አንድን ነገር አንቺ ልብ ሳትይው፣ እሱ አይቶ እንዴት ወደ ጨዋ ቀይሮ እንደሚያስቅ ስመለከት በጣም ይደንቀኝ ነበር፡፡ አንዳንድ ጊዜ ከስራ በኋላ ጊዜ ሲኖር ስንሰበሰብ ወጣቱን፣ ጎልማሳውን፣ አዛውንቱን እኩል የማሳቅ፣ የማጫወትና የማዝናናት ክህሎት ነበረው፡፡ እንደው የሚያውቁትን ሁሉ በአካል አግኝተሽ ስለሱ ብትጠይቂያቸው ብዙ የምትሰሚያቸው አስገራሚ ነገሮች ይኖራሉ፡፡     

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 19 July 2014 12:01

የጸሐፍት ጥግ

ፀሃፊዎች መድኃኒት አያዙም፤ ራስ ምታት እንጂ።
ቺኑዋ አቼቤ
(ናይጄሪያዊ ደራሲ፣ ገጣሚና ወግ ፀሃፊ)
ትንሽ ልጅ ሳለሁ ውሸታም ነበር የሚሉኝ፡፡ አሁን ስድግ ግን ፀሃፊ ይሉኛል፡፡
አይሳክ ባሼቪስ ሲንገር
(ትውልደ-ፖላንድ አሜሪካዊ ፀሃፊ)
ተሰጥኦ ብቻውን ፀሃፊ አያደርግም፡፡ ከመፅሃፉ ጀርባ ሰው መኖር አለበት፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኤመርሰን
(አሜሪካዊ ገጣሚና ወግ ፀሃፊ)
ፀሃፊ በመሞት መሆኑን ማሰቡ ጥሩ ይመስለኛል፡፡ ጠንክሮ እንዲሰራ ያተጋዋል፡፡
ቴኒሲ ዊሊያምስ
(አሜሪካዊ ፀሃፌ ተውኔት)
ቶኒ ሞሪሰን ቴሌቪዥን እንደማትመለከት በቅርቡ አነበብኩ፡፡ እርሷ ከአሜሪካ ባህል ሙሉ በሙሉ ተፋታ ለምንድነው የእሷን መፅሃፍ የማነበው
ካሚሌ ፓግሊያ
(አሜሪካዊ ምሁርና ደራሲ)
እነዚህን መተየቢያ ማሽኖች ያስቀመጥኳቸው በዋናነት በአንድ ወቅት ፀሃፊ እንደነበርኩ ራሴን ለማስታወስ ነው፡፡
ዳሺል ሃሜት
(አሜሪካዊ የወንጀል ታሪኮች ፀሃፊ)
ሌንሱ ክፍት የሆነ ካሜራ ነኝ፡፡ ዝም ብሎ የሚቀርፅ፣ የማያስብ፡፡
ክሪስቶፈር አይሸርውድ
(ትውልደ-እግሊዛዊ አሜሪካዊ ፀሃፊ)
ግን ማነው አለቃ መሆን ያለበት? ፀሃፊው ወይስ አንባቢው?
ዴኒስ ዲዴሮት
(የፈረንሳይ ኢንሳይክሎፒዲያ አዘጋጅና ፈላስፋ)
የአሜሪካ ጸሃፊዎች ጥሩ ሳይሆን ታላቅ መሆን ይፈልጋሉ፡፡ ሁለቱንም ግን አይደሉም፡፡
ጎሬ ቪዳል
(አሜሪካዊ ደራሲና ወግ ፀሃፊ)
ህፃናትን የምትወድ ከሆነ ከደራስያን ጋር መግባባት ከባድ አይደለም፡፡
ማይክል ጆሴፍ
(እንግሊዛዊ አሳታሚ)

Published in የግጥም ጥግ

         የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከፍተኛ ኃላፊዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ተከትሎ አዲስ የተዋቀረው የባለስልጣኑ የማናጅመንት ቡድን ባለፈው ዓመት “ግምገማዊ ስልጠና” አካሂዶ ነበር፡፡ ግምገማው ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮችን፣ ከፍተኛ ኦፊሰሮችና ሌሎች ሰራተኞችንም ይጨምራል፡፡  የግምገማው ቦታ አዳማ ዩኒቨርሲቲ ነበር፡፡ መኝታ እንዲሁም ቁርስና እራትን የምንጠቀመው  በዩኒቨርሰቲው ውስጥ ሲሆን የመፀዳጃ ቤት፣ የሻወርና የምግብ ጥራት ችግር ነበረው፡፡ ይሄን ችግር ለበላይ ሃላፊዎች ስናቀርብ የተሰጠን ምላሽ አስገራሚ ነበር፡፡ “የምናካሂደው አብዮት ስለሆነ እንዲህ ያለ ችግር አንሰማም” ነበር የተባለው፡፡ እኛም  በዝምታ  ግምገማውን ቀጠልንበት፡፡
ግምገማው በየዘርፉ የተካሄደ ሲሆን ምንም እንኳን ሂደቱ አሰልቺ ቢሆንም ጠቃሚ ጉዳዮች የተነሱበት፣ ትችቶች የተሰነዘሩበት፣ የመተራረም ተመክሮ ነበር ማለት እችላለሁ፡፡
ከተነሱት አንኳር ሃሳቦች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል፡-
የኪራይ ሰብሳቢነት ችግሮቻቸውና መፍትሔዎቻቸው
ሰዎች ያለሙያቸው ይመደባሉ፡፡ ለምን?
ወገንተኝነት በተቋሙ ይስተዋላል፡፡ ለምን?
አስተዳደሩ ሁሉንም ሰራተኛ  እንደሌባ ያየዋል
የማይመለከታቸው ሰዎች ውጭ ሀገር ለስልጠና ይሄዳሉ፡፡ ለምን?
የሰውና የሃብት አስተዳደር እንዲሁም የኦፕሬሽን ዘርፍ አሰራሩን መፈተሸ አለበት
የፓርቲ አባልና አባል ያልሆነ እኩል መብት ይኑራቸው
ልምድ ያለው ሰራተኛ የሚለቀው አመራሩ ስላልተመቸው ነው፤ ደሞዝ ቀንሶ የሚለቅበት እንቆቅልሽ ይታይ
ለትምህርት ደረጃ ዋጋ ይሰጠው
የአስተዳደር ብቃት የሌላቸው ሰዎች በኃላፊነት ለምን ይመደባሉ? … ወዘተ
አስተዳደሩ ለእነዚህ አስተያየቶች የሰጠው ምላሽ ሁሉንም በሂደት አይተነው እንፈተዋለን የሚል ነበር፡፡ ጉድና ጅራት በስተኋላ ነው እንዲሉ በመጨረሻዎቹ ቀናት ያልጠበቅነው ነገር ተከሰተ፡፡ በአባ ገዳ አዳራሽ ውስጥ ነበርን፡፡ በዋና ዳይሬክተሩ መሪነት “የምታውቁትን አጋልጡ” የሚል ትእዛዝ ከመድረኩ ተሰነዘረ፡፡ ከመቅፅበት ለትወና የተዘጋጁ የሚመስሉ ሰዎች ከግራም ከቀኝም እጅ ማውጣት ጀመሩ፡፡ “እከሌ እንዲህ ነው፣እከሊት እንዲህ ናት” እያሉ የማጋለጥ ሂደቱን ተያያዙት፡፡ ለምሳሌ ያህል አንድ ሁለቱን ልጥቀስላችሁ፡-
“እከሊት ከደሞዟ በላይ ነው ወጪዋ፡፡ የምትለበሰው ልብስ በጣም ውድ ነው፡፡” ከወደ ግራ በኩል የተሰነዘረ አስተያየት ነበር፡፡
ከወደ ቀኝ በኩል መልስ ተሰጠ “አረብ ሀገር እህቶች ስላሉኝ ነው”
 “አናቅሽም እንዴ --- አሁን ተጣላን እንጂ ባንድ ወቅት ጓደኛዬ በነበርሽ ሰዓት ደሞዛችን አልበቃ ብሎን ሰልቫጅ ተራ ሄደን አልነበር ልብስ የምንገዛው!”
አሳፋሪና ቦታውን የማይመጥን ምልልስ ቀጠለ…
ከወደቀኝ በኩል ሁለተኛ እድል የተሰጠው ሰው “እከሌና እከሊትን ጨምሮ ገንዘብ ከየት እንዳመጡ አላውቅም የሆነ አክሲዮን አቋቁመዋል፡፡” ሲል ተናገረ፡፡
ከመድረኩ ትእዛዝ ተሰማ “አክሲዮን አቋቁማችኋል ከተባላችሁት መካከል አንዳችሁ መልስ ሰጡ”
 “አዎ በእርግጥ አክሲዮን ለማቋቋም ጀምረን ነበር፡፡ ነገር ግን ካፒታላችን ዝቅተኛ ስለሆነ ብዙም አልገፋንበትም፤ ከአመት በፊት ፈርሷል። ባይፈርስም ግን አቅም ካለን አክሲዮንም ሆነ የአክሲዮን ሼር ለመግዛት የሚከለክለን ህግ ያለ አይመስለኝም፡፡”
ግምገማ ሳይሆን ሃሜት ነው የሚመስለው፡፡ በእጅጉ ማስረጃ ላይ ያልተደገፈ ውንጀላ የበዛበትም ነበር፡፡  እኔ እስከሚገባኝ ድረስ አንድ ሰው በኪራይ ሰብሳቢነት ከተጠረጠረ የሚመለከተው ክፍል በምርመራ ሂደት አጣርቶ ወይ ነፃ ይሆናል ወይም ወደ ፍትሕ አካል ይተላለፋል፡፡ ከላይ የጠቀስኩት አካሄድ ግን በጣም ግራ የሚያጋባ ነበር፡፡
ውጤቱም ማናጅመንቱ እንደጠበቀው አልነበረም፡፡ አብዛኛው ነባርና ልምድ ያለው ሰራተኛ ሁኔታው ስላላማረው መሥሪያ ቤቱን እየለቀቀ ወጣ፡፡ አዳዲስ የተቀጠሩ ሰራተኞችም ለስልጠና የወጣውን ወጪ በመክፈል ሥራቸውን ለቀቁ፡፡ ከዚያም የፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ችግር ከደንበኞች ዘንድ መሰማት ጀመረ።
ከጥቂት ጊዜ በኋላ በቴሌቪዥን መግለጫ ተሰጠ፡፡ ጋዜጠኛ ጠየቀ፤ “ሰራተኞች በብዛት እየለቀቁ ነው፤ ለምን ይመስልዎታል?” ባለስልጣኑ መለሱ “በእርግጥ እየለቀቁ ነው፤ እኛ በኪራይ ሰብሳቢነት ላይ ከፍተኛ ዘመቻ እያካሄድን ነው፡፡ ይኸው አልመች ብሏቸው ነው የሚለቁት፡፡”
ጋዜጠኛው፤ “ምኑ ነው አልመች ያላቸው?”
ባለስልጣን “ሌብነት ላይ የምናካሂደው ዘመቻ!”፤ (ያለማስረጃ ሁሉም በሌብነት ተፈረጀ)
የግምገማው ሂደት የተበላሸው በወቅቱ ሁሉም የበላይ አመራር አካላት አዲስ በመሆናቸውና  የገቢ ሰብሳቢ መሥሪያ ቤቱን ሰራተኛ ሁኔታ ባለመረዳታቸው ይመስለኛል፡፡ አብዛኛውን ሰራተኛ እንደሌባ መፈረጃቸው ነገሩን አበላሽቶታል፡፡
አሁን ግን ብዙ ነገር የተረዱ ይመስለኛልና ባለፈው ሳምንት በአዋሳ የተጀመረው ግምገማ ጥንቃቄ የተሞላበትና ሰራተኛውን የሚያስበረግግ ሳይሆን የሚያርም፣ ሞራል የሚሰጥና ለመስሪያ ቤቱ የእኔነት ስሜት እንዲሰማው የሚያደርግ እንደሚሆን ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ስኬታማ የግምገማ ጊዜ እመኛለሁ!

Published in ህብረተሰብ

ይህን አጭር ጽሑፍ ለመፃፍ ስዘጋጅ የሮን ሃወርድ ፊልም የሆነውንና ራስል ክሮው የሚተውንበትን Beautyfull mind የተባለውን ፊልም እየተመለከትኩ ነበር፡፡ በፊልሙ ላይ ዋናው ገጸ ባህሪ ለፍቅረኛው ክዋክብትን  ሲያሳያት ይታያል፡፡
ድቅድቅ ባለው ጨለማ ውስጥ ከሚታዩት ክዋክብት መካከል አንዳንዶቹ በአሁኑ ጊዜ ህልውና እንደሌላቸው ያውቃሉ?
ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ ለምሳሌ ለእኛ ፕላኔት ምድር ቅርቡ የሆነው ኮከብ አልፋ ሴንቸሪ፣ ከኛ አራት የብርሃን አመታት ይርቃል፡፡ ይህ ማለት ብርሃን በሰከንድ ሶስት መቶ ሺህ ኪሎ ሜትር እየተጓዘ አራት አመታት ያህል የሚወስድበት እርቀት ሲሆን ይህ ርቀት በኪሎ ሜትር ሲለካ ከሰላሳ ስድስት ትሪሊዮን ኪሎ ሜትር በላይ ነው፡፡ ይህ ማለት አሁን የምናየው የኮከቡ ገጽታ አሁን ያለውን መልኩን ሳይሆን ከአራት የብርሃን አመታት በፊት የነበረውን ነው፡፡ ይህም ሊሆን የቻለው ከኮከቡ የዛሬ አራት አመት በፊት የተነሳው ብርሃን ከርቀቱ  የተነሳ እኛ ጋ የደረሰው አሁን በመሆኑ ነው፡፡ አሁን ያለውን የኮከቡን መልክ ለማየት አራት የብርሀን አመታት መጠበቅ አለብን። ምክንያቱም ብርሃኑ ከኮከቡ ዛሬ ቢነሳ እኛ ጋ የሚደርሰው ከአራት የብርሃን አመታት በኋላ ስለሆነ ነው፡፡ ይህ እንግዲህ ለእኛ ቅርቡ የሆነው ኮከብ ያለው ርቀት ሲሆን በሚሊዮን የብርሃን አመታት ከእኛ የሚርቁ ከዋክብት አሁን የምናየው መልካቸው ከሚሊዮን አመታት በፊት የነበረ ነው፡፡  ምናልባት በአሁኑ ሰዓት በእድሜ ብዛት ሞተው ወይም ፈንድተው ድምጥማጣቸው ጠፍቶ ሊሆን ይችላል፡፡
ነገሩ አጃኢብ ነው፡፡ ይበልጥ የሚያስገርመው ግን እርስ በእርሳቸው በብዙ መቶ ሺህ የብርሃን አመታት የሚራራቁ አራት መቶ ቢሊዮን ከዋክብትን የያዘው ሚልኪ ዌይ የተባለው የእኛ ስርዓተ ፀሐይ ወይም Solar System ያለበት ጋላክሲ ትልቅነት ነው፡፡ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ የስነ - ፈለግ ተመራማሪዎች ህዋ ላይ ያለ ደመና ይመስላቸው ነበር፡፡ ነገሩ በቢሊዮን የሚቆጠሩት ከዋክብት ክምችት መሆኑ የታወቀው በ1610 ጋሊልዩ ጋሌልይ በቴሌስኮፑ ካየው በኋላ ነበር፡፡
ይህ የእኛ ፀሐይ የምትገኝበት ጋላክሲ ከመቶ እስከ መቶ ሃያ ሺህ የብርሃን አመታት የሚርቅ ዲያሜትር አለው፡፡ እንግዲህ የአንድ የብርሃን ዓመት ርቀት ከዘጠኝ ትሪሊዮን ኪሎ ሜትር በላይ መሆኑን ልብ ይበሉ፡፡ የእኛ ፀሐይ በዚህ አይነቱ Spherical ወይም ዝርግ በሆነው ጋላክሲ ውስጥ Minor arm በተባለው ክልል ውስጥ ትገኛለች፡፡ ጋላክሲው ማይነር እና ሜጀር አርም በመባል የሚታወቁ ክልሎች አሉት፡፡ ፀሐይ ከGalactic Center ወይም ከጋላክሲው መሐል ክፍል ሃያ ሰባት ሺህ የብርሃን አመታት ትርቃለች፡፡ ፀሐይ ከነጭፍሮችዋ የጋላክሲውን ማዕከል ስትዞር ወይም Rotation Period ሁለት መቶ አርባ ሚሊዮን አመታት ይፈጅባታል፡፡ ፀሐይ ከሌሎች ከዋክብት ጋር ይህንን የሮቴሽን ዑደት ስትፈጽም በሰከንድ 220 ኪሎ ሜትር ባለው ፍጥነት እየተጓዘች ነው፡፡ ጋላክሲው በራሱ የሚንቀሳቀስ ሲሆን በሰከንድ 600 ኪሎ ሜትር ይጓዛል፡፡
የዚህ ጋላክሲ ዕድሜ 13.6 ቢሊዮን አመታት እንደሆነ ሲገመት የተፈጠረው ለመላው ዩኒቨርስ መፈጠር ምክንያት ከሆነው ትልቁ ፍንዳታ ወይም Big bang በኋላ ብዙም ሳይቆይ ነው፡፡
የዚህ ጋላክሲ ማዕከል የሆነውና በብዙ ቢሊዮን የሚቆጠሩት ከዋክብቶች የሚዞሩት ነገር ምንድነው ብለን ብንጠይቅ የምናገኘው መልስ A Masive Black hole የሚል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡
Black hole ምን ማለት እንደሆነ ለማብራራት ከባድ ቢሆንም ለመሞከር ያህል---የስበት ሃይሉ በጣም ሐይለኛ ከመሆኑ የተነሳ አንዴ ወደ ውስጡ የገባ አካል ለዘላለም ፈጽሞ የማይወጣበት፣ ዕድሜአቸውን የጨረሱ ክዋክብት መቃብር ሲሆን አንድ ብላክ ሆል ከ50 ቢሊዮን ፀሐዮች በላይ ሰልቅጦ አየሁ የሚል አይደለም፡፡
የዚህ ሚልኪ ዌይ የተሰኘው ጋላክሲ ጐረቤት የሆነው ጋላክሲ ኢንደሮ ሜዳ የሚባል ሲሆን የያዛቸው የክዋክብት መጠን ከሚልኪ ዌይ የሚተናነስ አይደለም፡፡
በነገራችን ላይ ጋላክሲው ሚልኪ ዌይ የሚለውን ስሙን ያገኘው ከግሪኩ Via እንደሆነ የዘርፉ ምሁራን ይናገራሉ፡፡ እንግዲህ ይህ ግዙፍ ጋላክሲ በዩኒቨርስ ውስጥ ከሚገኙት አምስት መቶ ቢሊዮን ጋላክሲዎች አንዱ ብቻ ነው፡፡  

Published in ህብረተሰብ
Page 6 of 16