በ2015 እኤአ ሞሮኮ ወደ የምታስተናግደው 30ኛው አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ በምድብ ማጣርያ የሚሳተፈው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዝግጅቱን በሃዋሳ እያደረገ ነው። ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ከአልጄርያ ጋር በአዲስ አበባ ስታድዬም በሚያደርገው ጨዋታ የምድብ ማጣርያውን የሚጀምረው ብሄራዊ ቡድኑ በሙሉ ብቃት እና ዝግጅት ማድረጉ ወሳኝ ነው። ከዚሁ ጨዋታ በፊት ከግብፅ አቻው ጋር የወዳጅነት ግጥሚያ ማድረጉም አቋሙን ለመፈተሽ ከፍተኛ እገዛ ይኖረዋል። ዋልያዎቹ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ በበጀት መልክ ቢያንስ እስከ 50 ሚሊዮን ብር የሚያስፈልጋቸው ቢሆንም የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ በዚህ ጉዳይ እየተሰራባቸው ስላሉ የስፖንሰርሺፕ ድጋፎች እና የገቢ ምንጮች በይፋ የገለፀው ነገር የለም። በፌደሬሽኑ ፅህፈት ቤት አካባቢ እየተፈጠሩ ያሉ የአሰራር ዝርክርክነቶችም የብሄራዊ ቡድኑን ዝግጅት እና የማጣርያ ተሳትፎ አጓጉል እንዳየደርጉ ስጋት አለ፡፡ በሃዋሳ የሚዘጋጁት ዋልያዎች የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የምድብ ማጣርያ የመጀመሪያ ጨዋታውን ከማድረጉ በፊት በዋና አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ለ31 ተጨዋቾች ጥሪ ተደርጓል ፡፡

ከቅዱስ ጊዮርጊስ 12 ፤ከኢትዮጵያ ቡና 6፤ ከደደቢት 6 ፤ እንዲሁም ከአዋሳ ከዳሽን እና መከላከያ አንድ አንድ ተጫዋቾቹ ሲመረጡ ከሀገር ውጪ ደግሞ 5 ተጠርተዋል። አሉላ ግርማ ፤ቢያድግልኝ ኤልያስ፤ ሰላሀዲን ባርጊቾ ፤አበባው ቡጣቆ ፤አንዳርጋቸው ረታ ፤ምንተስኖት አዳነ ፤ምንያህል ተሾመ ፤በሀይሉ አሰፋ ፤አዳነ ግርማ፤ ኡመድ ኡኩሪ እና ፍፁም ገብረ ማርያም ናትናኤል ዘለቀ ከቅዱስ ጊዮርጊስ የተመረጡት ናቸው፡፡ ከኢትዮጵያ ቡና ደግሞ ጀማል ጣሰው፤ ቶክ ጀምስ፤ ጋቶች ፓኖም ፤መስኡድ መሀመድ፤ ዳዊት እስቲፋኖስና አስቻለው ግርማ ሲመለመሉ ከደደቢት ክለብ ታደለ መንገሻ ፤አክሊሉ አየነው፤ ብርሃኑ ቦጋለ፤ ስዩም ተስፋዬ፤ ታሪክ ጌትነትና ሲሳይ ባንጫ ተመርጠዋል፡፡ ግርማ በቀለ ከአዋሳ ፤ሽመልስ ተገኝተው ከመከላከና አስራት መገርሳ ከዳሽን ቢራ ሌሎች ከአገር ውስጥ ክለቦች ለብሄራዊ ቡድኑ የተጠሩ ናቸው፡፡ ከኢትዮጵያ ውጭ ባሉ ክለቦች የሚጫወቱት አምስቱ ተጨዋቾች ደግሞ ጌታነህ ከበደ ከደቡብ አፍሪካው ክለብ ቢድቪስት ዊትስ፤ ሰላሀዲን ሰኢድ ከግብፁ ክለብ አል አህሊ፤ ፍቅሩ ተፈራ በደቡብ አፍሪካ ክለቦች የተጫወተ እና አሁን ክለብ የሌለው ፤ከግብፁ አል ኢትሃድ ጋር ስሙ የተያያዘው ሽመልስ በቀለ እንዲሁም አዲስ ህንፃ ከሱዳኑ ክለብ አልአህሊ ሸንዲ ናቸው፡፡

ባሬቶ ምን ይጠበቅባቸዋል የእግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ ከወራት በፊት ዋና አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ቅጥራቸውን ሲፈፅሙ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በ2015 እኤአ ለሚደረገው የሞሮኮው 30ኛው አፍሪካ ዋንጫ ማሳለፋቸው ይጠበቃል ከማለታቸውም በላይ በአፍሪካ ዋንጫው ገብቶ መሳተፍ ብቻ ሳይሆን ከምድብ ፉክክር ባሻገር ለግማሽ ፍፃሜ በመድረስ የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ እንደሚጠበቅባቸው ማሳሰባቸው አይዘነጋም፡፡ ማርያኖ ባሬቶ ለምድብ ማጣርያው ዋና ዝግጅታቸውን በጀመሩበት ሰሞን በሰጡት መግለጫ ለ2015 የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ቃል እገባለሁ፤ ግን ፈታኝ ሂደትን በብቃት ለመወጣት መዘጋጀት አለብን ሲሉ ተናግረዋል፡፡ የመጀመርያዋ ተጋጣሚ አልጄርያ የዓለም ዋንጫ ጀብዷ እና ክብደቷ የኢትዮጵያ ብሔራዊ እግር ኳስ ቡድን (ዋልያዎቹ) በ2015 እኤአ ሞሮኮ ለምታስተናግደው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ በሚደረገው የምድብ ማጣርያ በምድብ 2 ከአልጄርያና ከማሊ የተገናኘ ሲሆን የምድቡ አራተኛ ቡድን በሁለተኛ ዙር ማጣርያ ከሚገኙት ቤኒና ማላዊ አንዱ ይሆናል፡፡ ኢትዮጵያ የምድብ ማጣርያውን የምትጀምረው በሴፕቴምበር 5 እና 6 በሜዳዋ ከአልጄርያ ጋር በምታደርገው ጨዋታ ነው፡፡

ይህ ጨዋታ ለዋልያዎቹ እና ለአዲሱ አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ መልካም አጀማመር ወሳኝ ይሆናል፡፡ በዚሁ የምድብ 2 የማጣርያ ጨዋታ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ባለው ሰፊ የዝግጅት ጊዜ በአካል ብቃት እና በአቋም መፈተሻ ግጥሚያዎች የተጠናከረ ሊሆን ይገባዋል፡፡ አልጄርያ በብራዚል በሚደረገው 20ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ተሳታፊ መሆኗ የግጥሚያውን ክብደት የሚያሳይ ነው፡፡ አልጄርያ በዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ ምእራፍ በመድረስ አዲስ ታሪክ ከመስራቷም በላይ በአጨዋወት ደረጃዋ ከፍተኛ ብቃት ማሳየቷ ተቀናቃኝነቷን ያጎላዋል፡፡ አልጄርያውያን ተጨዋቾች በዓለምን ዋንጫ ተሳትፏቸው ከፊፋ ያገኙትን 9 ሚሊዪን ዶላር በጋዛ ለሚኖሩ ፍልስጤማውያን በመለገሳቸውም በአረቡ አለም አድናቆት አትርፈው ዝናቸው ገንኗል፡፡ ቦስናዊው የብሄራዊ ቡድኑ አሰልጣኝ ቫልሂዝድ ከዓለም ዋንጫው በኋላ ስራቸውን በክብር ለቅቀው የቱርኩን ክለብ ትራብዞንስፖር ተረክበዋል፡፡ የአልጄርያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ምትካቸውን በሁለት ሳምንት ጊዜ ውስጥ የቀጠረ ሲሆን የ59 ዓመቱ ፈረንሳዊ ክርስትያን ጉርኩፍ ናቸው፡፡ አልጄርያን ለ2015፤ እና ለ2017 የአፍሪካ ዋንጫ እንዲያበቁ እና በ2018 ራሽያ ለምታስተናግደው 21ኛው ዓለም ዋንጫ እንዲያሳልፉ ኮንትራት ተሰጥቷቸዋል። ዮሃን ጉርኩፍ በፈረንሳይ ክለቦች እና እግር ኳስ የ25 አመት የአሰልጣኝነት ልምድ ያካበቱ ሲሆኑ በአልጄርያ አሰልጣኝነት የመጀመርያ ወሳኝ ጨዋታቸው አዲስ አበባ ላይ ከኢትዮጵያ ቡድን የሚገናኙበት ነው፡፡ በዓለም ዋንጫው የተሳተፉት 23 የአልጄርያ ተጨዋቾች መካከል 17 ያህሉ ትውልዳቸው በፈረንሳይ ሲሆን በከግማሽ በላይ የሚሆኑት በአውሮፓ ታላቅ ሊጎች የተጫወቱበት ሰፊ ልምድ አላቸው፡፡

በጀት፤ የወዳጅነት ጨዋታ እና ዝግጅት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአስተማማኝ ሁኔታ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ማለፉን የሚያረጋግጠው በተሟላ ዝግጅት ለግጥሚያዎቹ ትኩረት መስጠት ከተቻለ ነው፡፡ ዋልያዎቹ በሜዳቸው የሚያደርጓቸውን ሶስቱንም ጨዋታዎች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ማሸነፍ አለባቸው፡፡ ከሜዳ ውጭ ከሚደረጉት ሶስት ጨዋታዎች ደግሞ አንድ ድል እና አንድ አቻ ውጤት ማስመዝገብ ይጠበቅባቸዋል፡፡ በ2018 እኤአ ራሽያ ለምታስተናግደው 21ኛው ዓለም ዋንጫ ለማለፍ በተለይ በአፍሪካ ዞን ከዚያ አስቀድመው በ2015 እኤአ ላይ በሞሮኮ እንዲሁም በ2017 እኤአ ላይ በሊቢያ የሚደረጉት 30ኛው እና 31ኛው የአፍሪካ ዋንጫዎች ላይ የሚገኝ ተሳትፎ የአህጉሩን ተወካዮች ይወስናሉ፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በ2015 እኤአ ለሚደረገው አፍሪካ ዋንጫ ለመብቃት እንደደረጃው ቢያንስ ከ25 እስከ 50 ሚሊዮን ብር በጀት እንደሚያስፈልገው ለመገመት ተችሏል፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ለብሄራዊ ቡድኑ ይህን በጀት ለሟሟላት ከቴሌቭዥን ስርጭት መብት፤ ከስታድዬም ትኬት ሽያጭ፤ ከተለያዩ የስፖርት ቁሳቁሶች ሽያጭ እና ከስፖንሰርሺፕ ድጋፎች ከሚያገኛቸው ገቢዎች ባሻገር በስፖንሰርሺፕ እንቅስቃሴዎች መስራት ቢጠበቅበትም ብዙም እንቅስቃሴ እያሳየ አይደለም፡፡

ብዙዎቹ የአህጉሪቱ ብሄራዊ ቡድኖች ወደ የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ በማጣርያው እስከ 5 ሚሊዮን ዶላር ወጭ ያደርጋሉ፡፡ እሰከ 90 ሚሊዮን ብር ማለት ነው፡፡ ለኢትዮጵያ ምሳሌ እንዲሆን በጎረቤት አገር ኬንያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የታዩ ርምጃዎችን መጥቀስ ይቻላል። የኬንያ ቡድን ከ10 ዓመታት መራቅ በኋላ ወደ የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎው ለመመለስ በከፍተኛ ትኩረት እየሰራ ነው፡፡ የዓመት በጀቱ ከ300 ሚሊዮን የኬንያ ሽልንግ በላይ ነው፡፡ ይህን በጀት ከእግር ኳስ ፌደሬሽን፤ ከመንግስት እና ከስፖንሰሮች በሚያሰባስበው ገቢ ይሸፍናል፡፡ ሃራምቤስታርስ የሚባለው ብሄራዊ ቡድኑ በታዋቂው የአገሪቱ የቢራ ጠማቂ ኩባንያ ኬንያ ብሪዌሪስ ሊሚትድ አብይ ስፖንሰርነት እየተደገፈ ሲሆን ፍላይ540 የተባለ የአገሪቱ አየር መንገድ ቡድኑ ለአፍሪካ ዋንጫ እንዲያልፍ 1 ዓመት በሙሉ የትጥቅ ድጋፍ እና የትራንስፖርት አገልግሎት በመስጠት ስፖንሰር ሊያደርገው ከስምምነት ተደርሷል፡፡ የሁለቱ ኩባንያዎች የስፖንሰርሺፕ ድጋፍ ለሃራምቤ ስታርስ እስከ 50 ሚሊዮን የኬንያ ሽልንግ ያስገኛል፡፡

           ከእያንዳንዱ ስኬታማ ወንድ በስተጀርባ ሴት ትኖራለች የሚለው አመለካከት ከዓለም ዋንጫው ጋር በተያያዘ ሲያነጋግር ሰንብቷል፡፡ የታዋቂ እግር ኳስ ተጨዋቾች ሚስቶች፤ እጮኛዎችና የፍቅር ጓደኞች የእንግሊዝ ሚዲያዎች ‹‹ዋግስ› የሚል ስም አውጥተውላቸዋል፡፡ ከዝነኛ ስፖርተኞች ጋር ግንኙነት ያላቸው ሴቶች እንደማለት ነው፡፡ በዓለም ዋንጫው ሰሞን ሴቶቹ ከየብሄራዊ ቡድኑ ተጨዋቾች ጋር በነበራቸው ግንኙነት ዙርያ አሰልጣኞች ያወጧቸው አንዳንድ የስነምግባር ደንቦች አወዛግበዋል፡፡ በተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃናት የዝናቸው መጠን፤ ቁንጅናቸው፤ ለእግር ኳስ ባላቸው ፍቅር፤ ስለውድድሩ በሚሰጧቸው አስተያየቶች እየተነፃፀሩ ደረጃ ሲሰጣቸውም ነበር፡፡ ባሎቻቸውን ፤ እጮኛዎቻቸው እና ፍቅረኛዎቻቸውን ተጨዋቾችን ለማበረታት በየስታድዬሙ ማልያዎችን በመልበስ እና ባንዲራዎችን በማውለብለብ ድጋፍ በመስጠት ታውቀዋል። እነዚህ በዓለም ዋንጫው የደመቁ ሴቶች ልዩ ልዩ ሙያዎች ያላቸው ናቸው፡፡ ብዙዎቹ ሞዴሎች ናቸው። ተዋናዮች፣ ሙዚቀኞች፣ ጋዜጠኞችና የቤት እመቤቶችም ከመካከላቸው ይገኙበታል፡፡

ከጀርመን ጀርባ የነበረው ምስጥራዊ ግብረኃይል የጀርመን ብሄራዊ ቡድን 20ኛውን ዓለም ዋንጫ አሸንፎ በተሸለመበት የመዝጊያ ስነስርዓት የተጨዋቾች ሚስቶች፤ ፍቅረኛዎች፤ ጓደኞች እና ቤተሰቦች በጋራ ደስታቸውን ሲገልፁ መላው ዓለም በትዝብት የተከታተለው ነበር፡፡ በጀርመን ቡድን ዙርያ የተሰባሰቡት እነዚህ ሴቶች በዓለም ዋንጫው ተሳታፊ ቡድኖች ከታዩ ድጋፎች እንደተሳካላቸው የተለያዩ ዘገባዎች አውስተዋል፡፡ ዴይሊ ሜል ባቀረበው ዘገባ እንዳብራራው ለዓለም ዋንጫ ስኬት የቡድን አንድነት እና የላቀ ብቃት እንዲሁም የአሰልጣኞች የታክቲክ ፍልስፍና ከፍተኛ አስተዋፅኦ ቢኖራቸውም ፆታዊ ፍቅር የማይናቅ ሚና እንደነበረው የጀርመን ድል አረጋግጧል፡፡ የጀርመን ተጨዋቾች ሴቶቻቸውን ቁጥር አንድ ደጋፊዎቻን እያሉ ሲጠሯቸው ነበር፡፡ የተጨዋቾች ሚስቶች፤ ፍቅረኞች እና ቤተሰቦች የሻምፒዮናነት ሜዳልያውን በማጥለቅና ከሻምፒዮኖቹ ጋር ፎቶ በመነሳት እድለኞች ነበሩ። አንዳንዶቹ እንደውም ዋንጫዋን በመንካት እና በማቀፍ የማይገኝ ታሪክ ሰርተዋል፡፡ ከጀርመን የዓለም ዋንጫ ድል በኋላ በነበረው ፓርቲ ከፍተኛ ትኩረት አግኝተው ከነበሩ ዝነኛ ሴቶች ግንባር ቀደሟ በዋንጫው ጨዋታ ለጀርመን ድጋፍ የሰጠችው በርባዶሳዊቷ ሙዚቀኛ ሪሃና ነበረች፡፡

ሪሃና ከጀርመን ተጨዋቾች ጋር ባላት የቀረበ ግንኙት ከሻምፒዮናዎች ጋር አብራ መዝናናቷን ያወሳው ዴይሊ ሜል ጋዜጣ፤ ዓለም ዋንጫዋን በመንካት የፊፋ ስነምግባር እስከመተላለፍ መድረሷን በመጥቀስ ትችት አቅርቦባታል፡፡ ፊፋ ዓለም ዋንጫን ከመንግስታት መሪዎች ከአሸናፊ ብሄራዊ ቡድን አባላት በስተቀር ማንም እንዳይነካ የሚከለክል የስነምግባር ደንብ ነበረው፡፡ ሪሃና ግን ወደ ጀርመን ብሄራዊ ቡድን ሰርጋ በመግባት እንደፈለገች ፎቶዎች ተነስታ በሶሽያል ሚዲያ አሰራጭታለች፡፡ ሚሮስላቭ ክሎሰ፤ ሽዋንስታይገር እና ፖዶሎስኪ ዋና ምክንያቶች ነበሩ፡፡ ሜሲቲ ኦዚል ማልያውን አውልቆ ለሪሃና እንደሸለማትም ዴይሊ ሜል አትቷል፡፡ ጀርመን ዓለም ዋንጫውን ያሸነፈችበትን ግብ ያስቆጠረው ማርዮ ጎትዜ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ፍቅረኛውን አን ካተሪን ብሮሜል ፍቅሩን እየገለፀ በተደጋጋሚ ሲያመሰግናት ታይቷል፡፡ ‹‹በዚህ ታሪካዊ ድል የቤተሰቤ እና የፍቅረኛዬ አና ድጋፍ ልዩ ነበር፡፡ ሁሉም በእኔ ውጤታማነት ሙሉ እምነት ነበራቸው›› በማለት ማርዮ ጎትዜ የሴቶቹን ሚና ገልፆታል። ጎትዜ የጎሏን ያገባው መታሰቢያነት ለዚህችው የ25 ዓመት እጮኛው አድርጓታል፡፡

አና ካተሪን ብሮሜል በጀርመን የተሳካላት ሞዴል ስትሆን በፒያኖ ተጫዋችነትም እየታወቀች ነው፡፡ ዓለም ዋንጫውን ያደመቁት ሌሎች ሴቶች ጀርመንን የደገፉ ሴቶች በድል አድራጊነት ቢንበሻበሹም በዓለም ዋንጫው በርካታ ሴቶች በየሚደግፏቸው ብሄራዊ ቡድኖች ድምቀት ፈጥረዋል፡፡ የጣሊያኑ አጥቂ ማርዮ ባላቶሊ ዓለም ዋንጫው ሳይጀመር በዋዜማው ሰሞን እጮኛውን በማግኘቱ ቀዳሚውን ትኩረት መሳብ ችሎ ነበር፡፡ 100ሺ ፓውንድ በሚያወጣ ቀለበት ፋኒ ኔጉሻ ከተባለች ፍቅረኛው ጋር የተተጫጨው በብራዚል የባህር ዳርቻ ላይ ነው፡፡ ፋኒ የራሷ ስም የተፃፈበትን የጣሊያን ማልያ በመልበስ ሁሉንም የምድብ ጨዋታዎች ከሌሎች የጣሊያን ተጨዋቾች ሚስቶች እና ፍቅረኛሞች ጋር በየስታድዬሙ በመገኘት ተከታትላለች። ከሮናልዶ ጋር የፍቅር ጓደኝነት ከጀመረች 4 ዓመታት ያስቆጠረችው የ28 ዓመቷ ሩስያዊት ሱፕር ሞዴል ኤሪና ሻይክ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች በተሰጣት ሽፋን በቁንጅናዋ፤ በገቢዋ ከፍተኛነት የሚወዳደራት አልነበረም፡፡ የስፔን ብሄራዊ ቡድን ተከላካይ የሆነው ጄራርድ ፒኬ ጋር በፍቅር ጓደኝነት ከተሳሰረች 11 ዓመት ያለፋት ሻኪራ ደግሞ ዓለም ዋንጫ በሙዚቃዋ የገነነችበት ሆኗል፡፡ በ2010 እኤአ ለዓለም ዋንጫ ዜማ የነበረውን ዋካ ዋካ የሰራችው ሻኪም ለእግር ኳሱ ዓለም በመቅረብ የሚፎካከራት የለም፡፡ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ የመዝጊያው ስነስርዓት ላይ ደግሞ የሙዚቃ ኮንሰርቱ ዋና ሙዚቀኛ ኮሎምቢያዊቷ ስትሆን፤ በ2006፣ በ2010 እና በ2014 እ.ኤ.አ ላይ በተከናወኑት የዓለም ዋንጫ የመዝጊያ ስነስርዓቶች ሙዚቃ በማቅረብ የመጀመርያ ሆናለች፡፡ ኮሎምቢያዊቷ በ2010 እ.ኤ.አ የሠራችው “ዋካ ዋካ” የተሰኘው የዓለም ዋንጫ መሪ ዜማ ከዓለም ዋንጫ ዘፈኖች ከፍተኛውን ሽያጭ ያገኘ ነው፡፡ ሻኪራ በመላው ዓለም የአልበሞቿን 70 ሚሊዮን ቅጂዎች በመሸጥ የተሳካላት የላቲን ሙዚቃ ንግስት ናት፡፡

የሊዮኔል ሜሲን የበኩር ልጅ ቲያጐን የወለደችው አንቶኔላ ሬኩዞ በዓለም ዋንጫው ከታዩ እናቶች ተወዳጅነት ያተረፈችው ናት፡፡ ሜሲ 27ኛ ዓመት የልደት በዓሉን ከኢራን ጋር በተደረገ ጨዋታ ላይ አንድ ጎል አስቆጥሮ ሲያከብር አንቶኔላ ከልጃቸው ጋር በስታድዬም ተገኝታ ደስታዋን ገልፃለች፡፡ እስከፍጫሜው ድረስም አንድም የአርጀንቲና ጨዋታ አላመለጣትም፡፡ የዋይኔ ሩኒ የትዳር አጋር የሆነችው ኮሊን ሩኒ ሌላዋ አነጋጋሪ ሴት ናት፡፡ ኮሊን በራሷ ወጭ በዓለም ዋንጫው ሰሞን ካይ እና ክሌይ የተባሉ ሁለት ልጆቿን ይዛ ብራዚል በመገኘት ድጋፍ የሰጠች ነበረች፡፡ የ28 ዓመቷ ኮሊን ከእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ሚስቶች ወጭዋን ሸፍና ብራዚል በመጓዝ እና በአሳፋሪ ውጤት በጊዜ በመመለስ የምትጠቀስ ሆናለች፡፡ አብረዋት የ4 ዓመት ልጃቸው ካይ እና ገና 1 ዓመት የደፈነው ሌላ ወንድሙን ይዛ እንግሊዝ በመጨረሻው የዓለም ዋንጫው የምድብ ጨዋታ ከውድድር ውጭ ስትሆን ታድመዋል፡፡ ታዳጊ ሞዴል የሆነችው የኔይማር ጓደኛ ብሩና ማርኪውዚን፤ የዌስሊ ሽናይደር ሚስትና በሙያዋ ተዋናይት የሆነችው ዮላንቴ ሽናይደር ካቡ፤ እንዲሁም ታዋቂ ጋዜጠኛ የሆነችው የኤከር ካስያስ ሚስት ሱዛን ካርቦኔ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ስማቸው ከተነሱ ሴቶች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ የፈረንሳይ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ሚስቶች እና ፍቅረኞች ቡድናቸው ስታድዬም ገብተው በመደገፍ ተደንቀዋል፡፡

የባካሪ ሳኛ እና የፓትሪስ ኤቭራ ሴቶች በአስጨፋሪነታቸው አልተቻሉም ነበር፡፡በኡራጋይና ጣሊያን ብሄራዊ ቡድኖች የሚገኙ ተጨዋቾች ግንኙነት ያላቸው ሴቶች ያረፉባቸው በየአቅራቢያቸው የሚገኙ ባለ አምስት ኮከብ ሆቴሎች ናቸው። የሆላንዱ አሰልጣኝ ሊውስ ቫንጋል በአንዳንድ ግጥሚያዎች ዋዜማ ለተጨዋቾቻቸው ከቤተሰባቸው ጋር የሚገናኙበትን እረፍት በመፍቀድ ልዩ ውሳኔ አድርገዋል፡፡ የፍቅር ግንኙነት ይጠቅማል፤ ይጎዳል? ከዓለም ዋንጫ ጋር በተያያዘ ስለ ሴቶቹ መዘገብ የተጀመረው ውድድሩ ከመጀመሩ ሁለት እና ሶስት ወራት ቀድሞ ነበር፡፡ ከ32 ብሄራዊ ቡድኖች መካከል አብዛኛዎቹ የተጨዋቾች ሚስቶች፤ እጮኛዎችና ጓደኞች በዓለም ዋንጫው ስለሚኖራቸው ሚና የተለያዩ መመርያዎች አውጥተዋል፡፡ አንዳንድ አሰልጣኞች ከቡድናቸው አቅራቢያ ሴቶች፤ ልጆችና ሌሎች የቤተሰብ አባላት መኖራቸው ተጨዋቾች የልምምድ ሰዓቶችን እንዳያከብሩ፤ በተለያዩ ሁኔታዎች ሃሳብ እንዲገባቸው እና ትኩረታቸውን እንዲያጡ ያደርጋል የሚሉ ምክንያቶችን በመደርደር ጥብቅ ደንቦችን ለማውጣት ተገደዋል፡፡ ተጨዋቾች ከሚስቶቻቸው፤ ከፍቅረኞች እና ከሴት ጓደኞቻቸው ጋር በየጨዋታው ዋዜማ የወሲብ ግንኙነት የሚገድቡ ደንቦች አወዛግበዋል፡፡ አንዳንድ አሰልጣኞች ተጨዋቾች ማናቸውንም የፍቅር ግንኙነት ማድረጋቸው ውጤት ያበላሻል የሚል አቋም ነበራቸው፡፡ የራሽያ፣ ቦስኒያ፣ ቺሊና ሜክሲኮ አሰልጣኞች ምሳሌ ናቸው፡፡

ሌሎች ደግሞ ተጨዋቾች በነፃነት የፈለጉትን እንዲያደርጉ ፈቅደዋል፡፡ ጀርመን፣ ስፔን፣ አሜሪካ፣ አውስትራሊያ፣ ጣሊያን፣ ሆላንድ፣ ስዊዘርላንድና ኡራጋይ ናቸው፡፡ የቦስኒያ እና ሜክሲኮ አሰልጣኞች ከጨዋታ በፊት የሚፈፀም የወሲብ ግንኙነት የአካል ብቃት ያጓድላል በሚል ሲከለክሉ የትኛውም ፕሮፌሽናል ተጨዋች ያለ ወሲብ አንድ ወር ቢያሳልፍ ምንም ችግር አይፈጠርበትም በሚል መከራከርያ ነው፡፡ የብራዚል አሰልጣኝ የነበሩት ሊውስ ፍሊፕ ስኮላሬ በበኩላቸው ክልከላውን ቢደግፉም መመርያቸውን ለዘብ በማድረግ ተጨዋቾች ወሲብ ከፈፀሙ ከልክ ባለፈ ሁኔታ እንዳይሆን በማሳሰብ ነበር፡፡ የስፔን አሰልጣኝ ቪሴንቴ ዴልቦስኬ ማናቸውም ግንኙነት ግጥሚያ በሌለባቸው የእረፍት ቀናት ብቻ እንዲሆን ሲፈቅዱ የአውስትራሊያ፤ የፈረንሳይ እና የአሜሪካ አሰልጣኞች በበኩላቸው በተለያየ ደረጃ ቁጥብ ግንኙነት እንዲኖር አሳስበዋል፡፡

የናይጄርያው አሰልጣኝ ስቴፈን ኬሺ በበኩላቸው ትዳር የመሰረቱ ተጨዋቾች ከሚስቶቻቸው እና ቤተሰባቸው ጋር ግንኙነት እንዲኖራቸው ቢፈቅዱም ከማንኛውም የሴት ጓደኛ ወይም ፍቅረኛ ለሚደረግ ግንኙነት ግን ፈቃድ አልሰጥም ብለዋል፡፡ የቺሊ አሰልጣኝ ደግሞ ተጨዋቾቻቸው ቡድናቸውን ለጥሎ ማለፍ ምእራፍ ካበቁ በኋላ ለማናቸውም ግንኙነት ነፃነት ሰጥተዋል፡፡ የሆላንዱ አሰልጣኝ ሊውስ ቫንጋል ደግሞ ቡድናቸው ያለፈው ዓለም ዋንጫ ሻምፒዮኗን ስፔን 5ለ1 ካሸነፈበት ጨዋታ በፊት ተጨዋቾቹ ባረፉበት ሆቴል ሚስቶቻቸው፤ ፍቅረኞቻቸው እና ጓደኞቻቸው የጉብኝት ሰዓት እንዲፈቀድላቸው በመወሰናቸው ተሳክቶላቸዋል፡፡ ብዙ የእግር ኳስ አሰልጣኞች ከጨዋታ በፊት ተጨዋቾች ወሲብ ማድረግ የለባቸውም የሚል አመለካከትን ይቀበሉታል፡፡ ከጨዋታ በፊት ወሲብ መፈፀም የተጨዋችን ጉልበት ያባክናል፣ ኃይል ያሳጣል እንዲሁም የስነልቦና ዝግጅትን ያቃውሳል በሚልም ያስረዳሉ፡፡ አንዳንዶች ግን የሴቶቹ በዓለም ዋንጫ አካባቢ መገኘት ተጨዋቾች በሞራል እንዲነቃቁ ያደርጋል በሚል እምነት ሰርተዋል፡፡ ስታድዬም ገብተው ድጋፍ የሚሰጡበትን እድል እንደሚፈጥር እና ዝነኛ ሴቶች ከሆኑ ደግሞ የብሄራዊ ቡድኖችን ማልያ በማስተዋወቅ፤ የሚዲያ ሽፋን በማግኘት ብዙ መልካም ገፅታዎችን በመፍጠር ያላቸው አስተዋፅኦ መናቅ እንደሌለብትም የሚያስረዱ አሉ፡፡

    “...ያለችኝ ልጅ አንድ ነች፡፡ እኔ ግን ሌላ ልጅ ብወልድ ደስ ይለኝ ነበር፡፡ እኔ በአንድ ልጅ የቀረሁበትን ምክንያት ማስረዳት አልችልም፡፡ ነገር ግን ልጄን በወለድኩ በአንድ አመት ከስድስት ወሬ ሌላ ጸንሼ ነበር። አ.አ.ይ. አይሆንም፡፡ ይሄማ በላይ በላይ ይሆናል። እንዴት ላሳድግ ነው ስል... ባለቤቴ ግን ተይ ይወለድ አለኝ፡፡ አንተማ ምን ቸገረህ... የምሰቃየው እኔ ነኝ ብዬ አሻፈረኝ ብዬ ጽንሱ እንዲጨናገፍ አደረግሁ፡፡ ከዚያ በሁዋላ ግን የእርግዝና ነገር እርም ሆነ፡፡ እንዲያው ብቻ... የወር አበባዬ ዝብርቅርቅ አለ፡፡ ባሰኘው ጊዜ ይመጣል፡፡ ባሰኘው ጊዜ ይሄዳል፡፡ ሁለት ሶስር ወርም ድረስ ሳይፈስ ይቆያል፡፡ አሁን ማርገዜ ነው ብዬ ሳስብ ይፈሳል፡፡ አሁን እንኩዋን ጭርሱንም ቀርቶአል፡፡ እኔም በእድሜዬ ወደአርባው የገባሁ ስሆን ይሔው በአንድ ልጅ ቀርቻለሁ፡፡” እስከዳር ቢተው ከኮተቤ ወ/ሮ እስከዳር ያነሱት ጉዳይ በትክክል ምክንያቱ ይህ ነው ለማለት ባንደፍርም ነገር ግን የወር አበባቸው እንዳሻው መምጣት መቅረቱ የወር አበባ መዛባት የሚባለውን የስነ ተዋልዶ ጤና እንድናነሳ ያስገድደናል። ሊዚህ እትም ለንባብ ያልነው ...ለመሆኑ የወር አበባ መዛባት ሲባል ምን ማለት ነው? ምክንያቱስ? በሚለው ዙሪያ ነው፡፡

ይህንን ሳስብ ዶ/ር ሙሁዲን አብዶ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ሲሆኑ በኢትዮ ጠቢብ ሆስፒታል ሐኪምና በቅዱስ ጳውሎስ ሜዲካል ኮሌጅ እና ሀያት ሜዲካል ኮሌጅ በመምህርነት ያገለግላሉ፡፡ ጥ/ የወር አበባ ተፈጥሮአዊ ሂደት ምን ይመስላል? መ/ የወር አበባ አንዲት ሴት ለአቅመ ሄዋን ከደረሰች ማለትም በእድሜዋ ከ14-16 አመት በላይ እና በስተመጨረሻውም እስከ ሀምሳ አመት እድሜ ድረስ ከጭንቅላት ጀምሮ እስከ ማህጸን ድረስ ባሉ የተለያዩ የሰውነት አካልዋ በመታገዝ በየወሩ የምታስተናግደው ተፈጥሮአዊ ሁኔታ ነው፡፡ አመጣጡም ከ21-35 ቀን ባሉ ቀናት ሲሆን በመጣበት ወቅት ከ2 እስከ ስምንት ቀን ሊቆይ የሚችል ሲሆን መጠኑም በአማካይ ከ30 ሚሊ ሊትር እስከ ሰማንያ ሚሊ ሊትር ያለምንም ሕመም ወይንም መስተጉዋጎል የሚፈስ ከሆነ ይህ ጤናማ አፈሳሰስ ይባላል፡፡ ጥ/ የወር አበባ መዛባት ሲባል እንዴት ይገለጻል? መ/ በወር አበባ መዛባት አገላለጽ ዋናው የወር አበባ መጠኑ መብዛቱ ነው፡፡

የመጠን መብዛት ሲባል በትክክለኛው ጊዜውን ጠብቆ የሚፈስ የወር አበባ መጠኑ የሚበዛበት አጋጣሚ ይኖራል፡፡ ነገር ግን አንዲት ሴት የወር አበባዋ መጠኑን ከመጨመር ባለፈ መልኩ በጣም ቀላ ያለ ወይንም ወፈር ያለ ሆኖ ቀደም ሲል ትጠቀምበት የነበረውን ሞዴስ መጠን ከፍ ሲያደርግ ወይንም ቶሎ ቶሎ እንድትቀይር ሲያስገድዳት ሁኔታው ወደ መዛባት ማምራቱን ያሳያል፡፡ ጥ/ የወር አበባ መብዛት ምክንያቱ ምንድነው? መ/ ምክንያቶቹ የተለያዩ ናቸው፡፡ አንደኛው ኦርጋኒክ የሚባል በማህጸን ውስጥ የሚታይ የማህጸን ችግር ወይንም ከማህጸን ውጭ በሆርሞን መዛባት ምክንያት ሊከሰት የሚችል ነው፡፡ ከማህጸን ችግር መመልከት ብንጀምር ... በማህጸን ግድግዳ ላይ የሚበቅል ማዮማ የሚባለው እጢ እና ሌሎችም እጢዎች የወር አበባን ከሚያበዙ ችግሮች መካከል ናቸው፡፡ ሌላው በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ታዳጊ አገሮች ከአባላዘር በሽታዎች ጋር ተከትለው የሚከሰቱ የኢንፌክሽን አይነቶች እንዲሁም የማህጸን የቆየ ኢንፌክሽን እና በእድሜያቸው ከፍ ያሉ ወይንም ልጅ የሆኑ ሴቶች ከማህጸን እንቁላል ማፍሪያ ወይንም ኦቫሪያን ቲዩመር የሚባሉት ሆርሞን በሚያመርቱት አማካኝነት የወር አበባን እጅግ እንዲበዛ ያደርጉታል፡፡ የወር አበባ መዛባትን በሚመለከት ሌላም አስተያየት ደርሶናል፡፡ “...እኔ ገና የወር አበባ ሲጀምረኝ ጀምሮ የፍሰቱ መጠንም ሆነ የሚመጣበት ጊዜ ተስተካክሎ አያውቅም። እናነ ጀከእኔ ጋር በጣም ነበር የምትጨነቀው፡፡ በሁዋላም ወደሐኪም ቤት ስትወስደኝ የተነገራት ነገር የልብ ችግር እንዳለብኝ እና መታከም እንዳለብኝ ነበር።

አሁንም ብዙም ተስተንክሎአል ባይባልም ነገር ግን በመጠኑ ደህና ነኝ፡፡ የሚገርመው ነገር የወር አበባ ከሌላ ሕመም ጋር የሚገናኝ መሆኑ ነው፡፡” ቤቲ ከፒያሳ ጥ/ የወር አበባ መዛባት ከውስጥ ደዌ በሽታዎች ጋር ይገናኛልን? መ/ የተለያዩ የውስጥ ደዌ በሽታዎች ለችግሩ በምክንያትነት ይጠቀሳሉ፡፡ የወር አበባ መርጋት አለመርጋትን ከሚቆጣጠሩ የሰውነት ክፍሎች ውስጥ ለምሳሌ የቆየ የጉበት በሽታ ያለባት ሴት ኢስትሮጂን የተባለው ንጥረ ነገር በትክክል እንዳይመረት ስለሚያደርግ የወር አበባን ሊያዛባ ይችላል፡፡ ከፍተኛ የሆነ የደም ግፊት ያለባቸው ሴቶችም በዚህ ችግር እንደሚጠቁ የታወቀ ነው፡፡ ከእንቅርት ጋር በተያያዘ የሚከሰት ታይሮይድ እንዲሁም የደም መርጋት ችግር ጋር በተያያዘ የወር አበባ መዛባት ሊከሰት ይችላል። ባጠቃላይም የወር አበባ መዛባት ወይንም የወር አበባ መጠን መብዛትና ጊዜውን አለመጠበቅ ሊከሰት የሚችለው በማህጸን የውስጥ ችግር ወይንም እንቁላል ማምረቻ አካባቢ እና በሌሎችም የውስጥ ደዌ እና አካል መታወክ ሊሆን እንደሚችል ግልጽ ነው፡፡

ባጠቃላይም የወር አበባ መዛባትን ችግር ስንመለከት ከራሱ ከማህጸን ወይንም ከእንቁላል ማፍሪያው ሊሆን ስለሚችል አንዲት ሴት የወር አበባዋ በመጠኑ ከወትሮው ለየት ብሎ ወይንም በዛ ብሎ ስትመለከት ወደሕክምና ባለሙያ በመቅረብ ምክንያቱን ማወቅ ይገባታል፡፡ ጥ/ የወር አበባ መዛባት ከእርግዝና ጋር ይገናኛልን? መ/ በመውለጃ እድሜ ክልል ውስጥ ያሉ ሴቶች ሊያውቁት የሚገባው ነገር ከእርግዝና ጋርም በተገናኘ የወር አበባ መዛባት ሊከሰት እንደሚችል ነው፡፡ እርግዝና ተከስቶ ነበር ወይ? ተከስቶ ከነበረስ የእርግዝናው ሁኔታ ምን ይመስላል? የወር አበባው የሚዛባው ከእርግዝና ጋር ተያይዞ ነውን? በእርግዝናው ወቅት ጽንስ ብቻ እያደገ ሳይሆን ሌላም ችግር ተከስቶ ሊሆን ስለሚችል ሁኔታውን ማወቅ ይገባታል፡፡ ጥ/ የወር አበባ ከሚመጣበት ውስን ቀን ጋር በተያያዘ መዛባቱ ሊከሰት ይችላልን? መ/ የወር አበባ የሚመጣበት ቀን ከ21-35 ቀን ድረስ ነው፡፡ ነገር ግን ከ21- ቀን በታች ሲሆን ማለትም በየ10/ ወይንም 15/ ቀኑ የሚፈስ ከሆነ ትክክል ያልሆነ ወይንም ጤናማ ያልሆነ አመጣጥ ነው፡፡ ይህ አይነት የወር አበባ ፍሰት የሚታየው አብዛኛውን ጊዜ በወር አበባው በመጀመሪያው እድሜ አካባቢ ወይንም የወር አበባ ሊቀር አካባቢ በአማርኛው ማረጥ ከሚባለው እድሜ ቀደም ብሎ ነው፡፡

እንደዚሁም ከወሊድ ወይንም ውርጃ ከተከሰተ በሁዋላ የወር አበባ መዛባት ሊከሰት ይችላል፡፡ ምክንያቱ ምንድነው? ስንል በወር አበባ ኡደት የሚፈልቁ ሆርሞኖች በትክክለኛው ጊዜያቸውን ጠብቀው ባለመምጣታቸው እና አንዱ ተቀብሎ ወደሌላኛው የሚያስተናግድበት ሂደት በመሰናከሉ ምክንያት ነው፡፡ ጥ/ ከወር አበባ መጠን ባለፈስ ለመዛባቱ በምክንያትነት የሚጠቀስ አለ? መ/ የወር አበባ መጠኑን ጠብቆ ቢመጣም ነገር ግን ባልተለመደ ሁኔታ እንዳሰኘው በ10/ ወይንም 15/ቀን እየተመላለሰ ድንገት ሊታይ ይችላል፡፡ የዚህም ምክንያቱ ከእድሜ ጋር በተያያዘ በተለይም እድሜያቸው ትንሽ ገፋ ያለ ሴቶች ላይ የሚከሰት የማህጸን በር ወይንም የማህጸን ካንሰር ወይንም በማህጸን ግድግዳ ውስጥ ከሚበቅሉ እጢዎች መንስኤነት የወር አበባ መዛባት ሊከሰት ይችላል፡፡ ጥ/ የወር አበባ ከ35/ቀን በላይ አሳልፎ ሲመጣ ምን ይከሰታል? መ/ ብዙውን ጊዜ እድሜያቸው ወደ ማረጥ የደረሱ ሴቶች የወር አበባ ጊዜያቸው ከ35/ቀን በላይ 40/እና ከዚያም በላይ ቆይቶ ሊመጣ ይችላል፡፡

ይህን አይነት ችግር የሚገጥማቸው ሴቶች በአብዛኛው ከሆርሞን መዛባት ወይንም ደግሞ ከክብደት ጋር በተያያዘ ወይንም በሕይወታቸው በጣም በሚያስጨንቅ ሁኔታ የሚኖሩ እንዲሁም የቆዩ ኢንፌክሽኖች ያለባቸው ሴቶች የወር አበባ መብዛትን ሊያስከትልባቸው ይችላል። እንደዚህ አይነት አጋጣሚዎች ሲከሰቱ ከሐኪም ጋር መመካከር ያስፈልጋል፡፡ ጥ/ የወር አበባ መጠን ማነስ ለወር አበባ መዛባት አስተዋጽኦ አለውን? መ/ አንዳንድ ጊዜ መጠኑ በጣም ያነሰ እንዲሁም የሚፈስበት ቀንም ከ2/ ቀን ያነሰ ሊሆን ይችላል። ለዚህም ምክንያት ከሚሆኑት መካከል በማህጸን ግድግዳ የወር አበባን ኡደት የሚያስተናግደው ክፍል ችግር ሲያጋጥመው፣ ኢንፌክሽኖች ወይንም የወር አበባ መቆጣጠሪያ ኪኒኖችን ለረጅም ጊዜ ተጠቅመው ከሆነ እና ከታይሮድ ጋር በተያያዘ እና በመሳሰሉት የሚከሰት ነው፡፡ ጥ/ አንዲት ሴት የወር አበባ መዛባት ሲያጋጥማት መውሰድ ያለባት እርምጃ ምንድነው? መ/ አንዲት ሴት የወር አበባ መዛባት ሲያጋጥማት በቀላሉ መመልከት የለባትም፡፡ መንስኤው ምን እንደሆነ ለማወቅ ወደህክምና ተቋም በመሄድ የህክምና ባለሙያውን ማማከር፣ ተገቢውን ምርመራና ሕክምና ማድረግ ይጠበቅባታል፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

     በኢትዮጵያ ስፖርት የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ለመሸለም የበቁት ለአገሪቱ ከፍተኛ ዝና እና ክብር ያስገኙት አትሌቶች ናቸው፡፡ ባለፉት ዓመታት በአገር ውስጥ እና የውጭ አገር ዩኒቨርስቲዎች የክብር ዶክትሬት ተሸላሚዎች የነበሩት ፈር ቀዳጆቹ አትሌቶች ኃይሌ ገ/ስላሴ እና ደራርቱ ቱሉ ናቸው። ባለፈው ሰሞን ደግሞ  ሁለት የኢትዮጵያ ዩኒቨርስቲዎች ለአትሌት መሠረት ደፋርና ጥሩነሽ ዲባባ የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎችን ሸልመዋል፡፡ ለሁሉም የክብር ዶክትሬት ዲግሪው ይገባቸዋል፡፡ ዘንድሮ ባለመሸለሙ የሚያስቆጨውና በቅርቡ መሸለሙ የማይቀረው የኢትዮጵያ ታላቅ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡
በመላው ዓለም የሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች፣ ኮሌጆችና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በማህበረሰብ ተሟጋችነታቸው፤ በበጐ አድራጊነታቸው፤ በጀግንነት ተግባራቸው፤ በስፖርት፣ የሙዚቃ ለኪነጥበብ በሰሯቸው ፈር ቀዳጅ ታሪኮችና ስኬቶቻቸው ለተመረጡ ግለሰቦች የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎችን ይሸልማሉ፡፡ በክብር ዶክትሬት ዲግሪዎች ተሸላሚነት ከሚጠቀሱ የሙያ መስኮች ደግሞ ስፖርተኞች ከፍተኛውን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡ የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎች የሚሰጡት ለከፍተኛ ስኬት እውቅና ለመስጠት እና ለማክበር ተብሎ ነው፡፡ ዩኒቨርሲዎቹ ለታላላቅ ስፖርተኞች የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎችን በመሸለም ለስኬታቸው ዕውቅና ይሰጣሉ፡፡ ተሸላሚዎቹ የክብር ዶክትሬት ዲግሪያቸውን ተቀብለው ንግግር ማድረጋቸውንም ይፈልጉታል፡፡ ከስኬታማ ስፖርተኞች ጋር ስማቸው እንዲነሳ በመፈለግም የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎችን ይሰጣሉ፡፡
የፈር ቀዳጆቹ ኃይሌ እና ደራርቱ የክብር ዲክትሬት ዲግሪዎች
ታላቁ ሯጭ ኃይሌ ገ/ስላሴ በዓለም አቀፉ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ከተሸለመው ልዩ “የኦሎምፒክ ኦርደር” ሽልማት ባሻገር አራት የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎችን ሁለት ከአገር ውስጥ እንዲሁም ሁለት ከውጭ አገር ዩኒቨርስቲዎች ተቀብሏል፡፡ የመጀመሪያውን የክብር ዶክትሬት ዲግሪ የተቀበለው በ2005 እ.ኤ.አ ላይ ከ‹‹ናሽናል ዩኒቨርሲቲ ኦፍ አየርላንድ›› ነበር፡፡ አትሌት ኃይሌ ይህን የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ለመሸለም የበቃው በስፖርቱ መስክ ካስመዘገባቸው ታላላቅ ስኬቶች ባሻገር በአገሩ የልማት እንቅስቃሴ ላይ ንቁ ተሳትፎ በማድረጉና በተለይ ለትምህርት ዘርፍ በተጫወተው ሚና እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ኃይሌ ከ‹‹ናሽናል ዩኒቨርሲቲ ኦፍ አየርላንድ›› የክብር ዶክትሬት ዲግሪውን ሲቀበል ባቀረበው ንግግር ሽልማቱ ወደፊትም ብዙ ለመስራት እንደሚያነሳሳው የተናገረ ሲሆን በዩኒቨርሲቲው የተገነባውን የስፖርት መሠረተ ልማት መርቆ የከፈተ የክብር እንግዳ ነበር፡፡ የኃይሌ ሁለተኛው የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሽልማት ደግሞ በ2008 እ.ኤ.አ ከ‹‹ሊድስ ሜትሮፖሊቲያን ዩኒቨርሲቲ›› የተበረከተለት ነው፡፡ የዩኒቨርሲቲው ኃላፊዎች ይህን የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ለኃይሌ የሸለሙት  16ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በአዲስ አበባ ለተከናወነበት ወቅት በአዲስ አበባ ስታድዬም በተደረገ ስነስርዓት ነው። የሊድስ ሜትሮፖሊቲያን ዩኒቨርሲቲ የስፖርት ዳይሬክተር በወቅቱ ስለ ኃይሌ መሸለም ንግግር ሲያረጉ “ኃይሌ አትሌት ብቻ ሳይሆን የአፍሪካ አምባሳደር” ነው ብለዋል፡፡ ኃይሌ ሌሎቹን ሁለት የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎች የተሸለማቸው  በ2010 እ.ኤ.አ ላይ ከአዲስ አበባና ከጅማ ዩኒቨርሲቲዎች ነው፡፡
ከኢትዮጵያ ሴት አትሌቶች 2 የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎች መቀበል የቻለችው ደራርቱ ቱሉ ናቸው፡፡ አንድ ከአገር ውስጥ እንዲሁም ሌላ ከውጭ አገር ዩኒቨርሲቲዎች የተቀበለቻቸው ናቸው፡፡  አትሌት ደራርቱ ቱሉ ከ4 ዓመት በፊት የመጀመሪያ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ የተሸለመችው በጅማ ዩኒቨርሲቲ ነበር። በ2012 እ.ኤ.አ ላይ ደግሞ ከደቡብ አፍሪካው “ዌስተርን ኬፕ ዩኒቨርሲቲ” ተሸልማለች፡፡ የዌስተርን ኬፕ ዩኒቨርሲቲ ለአትሌት ደራርቱ ቱሉ የክብር ዶክትሬቱን የሰጠው በአፍሪካ ሴቶች የኦሎምፒክ ተሳትፎ በወርቅ ሜዳልያ ስኬት ፈር ቀዳጅ ታሪክ ለመስራቷ እንደሆነ በወቅቱ ተገልጿል፡፡
መሲና ጥሩ የዘንድሮ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ተሸላሚዎች
ባለፉት ሁለት ሳምንታት በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ድንቅ ታሪክ በመስራት ከፍተኛ ዓለም አቀፍ ዝና ያገኙት ሁለት አትሌቶች የክብር ዶክትሬት ዲግሪያቸውን አግኝተዋል። አትሌት መሠረት ደፋርና አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ናቸው። የመጀመሪያዋ ተሸላሚ አትሌት መሠረት ደፋር የክብር ዶክትሬት ዲግሪ የተቀበለችው ከጐንደር ዩኒቨርሲቲ ነው። መሰረት ለዚህ ሽልማት የበቃችው በአትሌቲክስ ስፖርት የላቀ ውጤት በማስመዝገቧ ነው ተብሏል፡፡ ለመሠረት ደፋር ይሄው የክብር ሽልማት የመጀመሪያ ልጇን በወለደችበት ወር ውስጥ ነው፡፡ የ30 ዓመቷ አትሌት መሠረት ደፋር በዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ውድድሮች 11 ወርቅ፣ 7 የብር እና 4 የነሐስ ሜዳልያዎች ሰብስባለች፡፡ ከሳምንት በፊት ደግሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ  ለ28 ዓመቷ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ሸልሟታል፡፡ በ63ኛው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የምረቃ ስነስርዓት ላይ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ለክብር ዶክትሬት  የበቃችው በአትሌቲክስ ስፖርት በአገርና በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገቧ መሆኑ ተገልጿል፡፡ በኢትዮጵያ የኦሎምፒክ ተሳትፎ ታሪክ ከፍተኛው ስኬት ያስመዘገበችው ሴት አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ  ናት፡፡ በሩጫ ዘመኗ በዓለም አቀፍ አትሌቲክስ ውድድሮች 15 የወርቅ፣ 5 የብርና 2 ነሐስ ሜዳልያዎች የሰበሰበች ሲሆን የ5ሺ ሜትር የዓለም ሪኮርድ ከያዘች 8 ዓመት ሆኗታል፡፡
እነማን መሸለም ይገባቸዋል
አትሌት ቀነኒሳ በቀለ እና ከላይ የተጠቀሱት የኢትዮጵያ ምርጥ አትሌቶች ከክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሽልማት ባሻገር የአገሪቱን የክብር ኒሻን መሸለማቸው ትልቁ ክብር ነው፡፡ አትሌት ቀነኒሣ በቀለ በኢትዮጵያ የአትሌቲክስ ስፖርት ታሪክ ከፍተኛውን ውጤት ያስመዘገበ አትሌት መሆኑ ደግሞ ለክብር ዶክትሬት ዲግሪ ተሸላሚነት ዋናው ዕጩ ያደርገዋል፡፡
የ32 ዓመቱ አትሌት ቀነኒሣ በቀለ በረዥም ርቀት የአትሌቲክስ ውድድሮች በ10ሺና በ5ሺ ሜትር የዓለም ሪኮርዶችን ከያዘ ከ12 ዓመታት በላይ ተቆጥረዋል፡፡ በኦሎምፒክ 3 ወርቅ 1 የብር፤ በዓለም ሻምፒዮና 5 ወርቅና 1 ነሐስ፤ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮን 11 ወርቅ 1 የብር ሜዳልያዎች በመሰብሰብ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛውን የውጤት ክብረወሰን ያስመዘገበ ነው፡፡ በ2004 እና በ2005 እ.ኤ.አ በዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር የዓለም ኮከብ አትሌት ሆኖ አሸንፏል፡፡
በ1986 እ.ኤ.አ በሞስኮ ኦሎምፒክ ሁለት ድርብ የወርቅ ሜዳልያ ድሎችን ያስመዘገበው እና የኢትዮጵያን አትሌቲክስ ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገበ እንዲቀጥል  በተምሳሌትነት የሚጠቀሰው አንጋፋው አትሌት ምሩፅ ይፍጠር ሌላው የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ክብር የሚገባው ነው፡፡ ለረዥም ዘመናት የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ብሔራዊ ቡድን ለዋና አሰልጣኝነት የመሩት ዶ/ር ወልደመስቀል ኮስትሬም ያስፈልጋቸዋል፡፡ በኢትዮጵያ የኦሎምፒክ ተሳትፎ ታሪክ ፈርቀዳጅ ኦሎምፒያን የሚባለው እና በብስክሌት ስፖርት ግንባር ቀደም ታሪክ ያለው ገረመው ደንቦባም የሚጠቆም ነው፡፡ አንጋፋው አትሌት ምሩጽ ይፍጠር፤ ዋና አሰልጣኝ ዶ/ር ወልደመስቀል ኮስትሬ እና ገረመው ደንቦባ ለክብር የዶክትሬት ዲግሪ ተሸላሚነት ዋና እጩ ሆነው የሚጠቆሙት በህይወት ያሉ የኢትዮጵያ የስፖርት ጀግኖች በመሆናቸው ነው፡፡  ኢትዮጵያ ከ31 ዓመት በኋላ ከአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ እንድትበቃ ያስቻሉት፤ በቻን ውድድር ለመጀመሪያ ጊዜ እንድትሳተፍ ያደረጉት እና በዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ከፍተኛውን ውጤት እንድታስመዘግብ የሰሩት የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውም ለዚሁ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ክብር ቢበቁ የሚመሰገን ነው፡፡
የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ተሸላሚዎች በዓለም አቀፍ ደረጃ
በመላው ዓለም የሚገኙ ትልልቅ ዩኒቨርሲቲዎች ለዓለማችን ታላላቅ ስፖርተኞች የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎችን በተለያዩ ጊዜያት ሸልመዋል፡፡ የዓለማችን የምንጊዜም ታላቅ የእግር ኳስ ተጨዋች የሆነው ኤድሰን አራንተስ ዶናሺሜንቶ ፔሌ ከ2 ዓመት በፊት በአውሮፓ የመጀመሪያውን የክብር ዶክትሬት ዲግሪ የተቀበለው ከዓለም 20 ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ ከሆነው ኤደንብራ ዩኒቨርሲቲ ነው፡፡ ፔሌ ከአውሮፓ ውጭ በርካታ የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎችን ከተለያዩ የዓለም ክፍሎችም ተቀብሏል፡፡  የኤድንብራ ዩኒቨርሲቲ ለፔሌ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ የሸለመው በእግር ኳስ ስፖርት ካስመዘገበው ዘመን የማይሽረው ስኬት ባሻገር በሰብዓዊ መብት ተሟጋችነት እና በአካባቢ ጥበቃ እንቅስቃሴዎች የላቀ አስተዋጽኦ አበርክቷል በሚል ነው፡፡ታላቁ የማንችስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ሰር አሌክስ ፈርጉሰን በስራ ዘመናቸው 9 የክብር ዲግሪዎችን ከመላው የብሪታኒያ ዩኒቨርስቲዎች ተቀብለዋል፡፡ ፈርጊ ያገኙት የክብር ዲግሪዎች ብዛት በኤፍ ኤካፕ እና የሻምፒንስ ሊግ ውድድሮች ከሰበሰቧቸው ዋንጫዎች ብዛት ይበልጣል፡፡ ሰር አሌክስ ፈርጉሰን በማንችስተር ዩናይትድ በቆዩባቸው የስራ ዘመናት 12 የፕሪሚዬር ሊግ፤ ሁለት የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፤ 5 የኤፍ ኤካፕ እና 10 የሊግ ካፕ ድሎችን አስመዝግበዋል፡፡ ከፈርጊ የክብር ዲግሪዎች መካከል በ2011 እኤአ ላይ በዩኒቨርስቲ ኦፍ ማንችስተር የተሰጣቸው በማንችስተር ዩናይትድ 25 አመታት ግልጋሎት እውቅና የተሰጠበት ሲሆን በወቅቱ ስለተሰጣቸው ክብር ባሰሙት ንግግር ‹‹ መደነቅ እና መመስገን ሁሌም ያስደስታል፡፡ በታታሪነት እና ጠንክሮ በመስራት ለሚገኝ ስኬት እውቅና ማግኘት ክብር ነው፡፡›› ብለው ነበር፡፡ የፈርጉሰን ሌላኛው የክብር ዲግሪ በ2012 እኤአ  በዩኒቨርስቲ ኦፍ ኡሊስተር የተሰጣቸው ሲሆን ዶክተር ኦፍ ሳይንስ በሚል የተሰጣቸው የክብር ዶክትሬት በእግር ኳስ ስፖርት ለፈፀሙት ግልጋሎት የተበረከተ ነበር፡፡
ታዋቂው ቦክሰኛ ማይክ ታይሰንም በስፖርቱ ካገኘው ስኬት ባሻገር በመጥፎ በሀገር ውስጥ በወንጀሎቹ ቢወቀስም በ1986 እ.ኤ.አ ላይ በኦሃዮ የሚገኘው ሴንትራል ስቴት ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ተሸልሟል፡፡

20ኛው ዓለም ዋንጫ የምንግዜም ምርጥ እንደነበር የተለያዩ ዘገባዎች፤ የስፖርት መሪዎች እና ባለሙያዎች ገልፀዋል፡፡ ጀርመን ለ4ኛ ጊዜ የዓለም ሻምፒዮን በመሆን አስደናቂ ስኬት ያስመዘገበችበት ነው፡፡ የዓለም አቀፉ እግር ኳስ ፌደሬሽኖች ማህበር ‹ፊፋ› ፕሬዝዳንት  ሴፕ ብላተር ዓለም ዋንጫው ከ10 ነጥብ 9.25 እንደተሰጠው ተናግረዋል። የነጥቡን ስሌት የሰራው የፊፋ ቴክኒካል ኮሚቴ ሲሆን ከ4 ዓመት በፊት ደቡብ አፍሪካ አስተናግዳ የነበረችው 19ኛው ዓለም ዋንጫ ያስመዘገበው 9 ነጥብ ነበር፡፡
በ20ኛው ዓለም ዋንጫ አዘጋጅነት ብራዚል በሜዳ ላይ ውጤት ባይቀናትም በመሰናዶዋ ግን ትርፋማ መሆኗን እየገለፀች ነው፡፡ የብራዚል መንግስት ይፋ ባደረገው መረጃ  መሰረት በዓለም ዋንጫው ሰሞን  እስከ 600ሺ የተጠበቀው የቱሪስት ብዛት 1 ሚሊዮን ማለፉንና ከ202 የተለያዩ አገራት መምጣታቸው ታውቋል፡፡ ከዓለም ዋንጫው ጋር ተያይዞ  ከ3 ሚሊዮን በላይ ብራዚላውያን በመላው የአገሪቱን ክፍሎች እንደተዘዋወሩ ተገልፆ፤ በተለያዩ የብራዚል ከተሞች በርካታ ህዝብ በሚመለከትባቸው አደባባዩች ዓለም ዋንጫው 5 ሚሊዮን ተከታታዮች እንደነበሩት ተነግሯል፡፡
64 ጨዋታዎችን በብራዚል 12 ስታድዬሞች ተገኝተው የታደሙት ብዛታቸው 3 ሚሊዮን 429 ሺ 873 ሲሆን በየጨዋታው በአማካይ 53ሺ 592 ተመልካች ስታድዬም ይገኝ ነበር፡፡
ለዚህ የስታድዬም ማራኪ ድባብ ብራዚላውያን ከፍተኛ አስተዋፅኦ ነበራቸው፡፡ ዓለም ዋንጫ በስታድዬም ገብቶ ለመከታተል ብራዚላውያን 1.5 ሚሊዮን ትኬቶችን በመግዛት አንደኛ ነበሩ፡፡ በ1994 እኤአ ላይ አሜሪካ ባዘጋጀችው 15ኛው ዓለም ዋንጫ በ24 ቡድኖች መካከል ቢደረግም የተመዘገበው 69ሺ የስታድዬም ተመልካች ክብረወሰኑ ነው፡፡ 20ኛው ዓለም ዋንጫ በስታድዬም ተመልካች ብዛት በውድድሩ ታሪክ በሁለተኛ ደረጃ የሚጠቀስ ሆኗል፡፡
በዓለም ዋንጫው ከመጀመርያው የምድብ ማጣርያ ጨዋታ እስከ ዋንጫው በተደረጉ 64 ግጥሚያዎች 171 ጎሎች መመዝገባቸው በውድድሩ ታሪክ ከፍተኛው ሆኖ በክብረወሰን ተመዝግቧል፡፡171 ጎሎቹ የገቡት በ121 የተለያዩ ተጨዋቾች ነው፡፡ በአንድ ጨዋታ በአማካይ 2.67 ጎሎች ተመዝግበዋል፡፡
በ6 ጎሎቹ የዓለም ዋንጫ ኮከብ ግብ አግቢ በመሆን የጨረሰው የኮሎምቢያው ጀምስ ሮድሪጌዝ ሲሆን የወርቅ ጫማ ተሸልሟል፡፡ ቶማስ ሙለር በ5 ጎሎች የብራዚሉ ኔይማር በ4 ጎል የብር እና የነሐስ ጫማቸውን ተቀብለዋል፡፡ የወርቅ ጓንት የተሸለመው የጀርመኑ ግብ ጠባቂ ማኑዌል ኑዌር ሲሆን የኮስታሪካው ኬዬሎር ናቫስ እና የአርጀንቲናው ሰርጂዮ ሮሜሮ ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ አግኝተዋል፡፡ በኮከብ ተጨዋችነት ደግሞ የአርጀንቲናው ሊዮኔል ሜሲ ሲመረጥ ቶማስ ሙለር ከጀርመን እንዲሁም አርያን ሮበን ከሆላንድ የብር እና የነሐስ ኳሶችን ተሸልመዋል፡፡  የዓለም ዋንጫው ምርጥ ወጣት ተጨዋች የተባለው ደግሞ የፈረንሳዩ ፖል ፖግባ ሲሆን  ኮሎምቢያ የስፖርታዊ ጨዋነት ሽልማትን አሸንፋለች፡፡
ጀርመን የዓለም እግር ኳስ ተምሳሌት ሆናለች
 የጀርመን ብሄራዊ ቡድን ምእራብ እና ምስራቅ ጀርመን ከተዋሃዱ የመጀመርያውን ዓለም ዋንጫ ድል ማስመዝገቡ ነው፡፡ በአጠቃላይ ለአራት ጊዜያት የዓለም ሻምፒዮን በመሆን ከጣሊያን ብሄራዊ ቡድን ጋር በከፍተኛ የዋንጫ ስብስብ የሁለተኛ ደረጃን ተጋርቷል፡፡ በሌላ በኩል የአውሮፓ ቡድን በደቡብ አሜሪካ የተዘጋጀን ዓለም ዋንጫን ሲያሸንፍ በታሪክ የመጀመርያው ሆኖ ሲመዘገብ የአውሮፓ አህጉር በዓለም ዋንጫ ያስመዘገበውን የሻምፒዮናነት ክብር ወደ 11 አሳድጎታል። የደቡብ አሜሪካ ቡድን የሻምፒዮናነት ክብር በ9 ድሎች ተወስኖ ቀርቷል፡፡
ለጀርመን 4ኛው የዓለም ዋንጫ ድል ከ24 ዓመት በኋላ የተመዘገበ ስኬት ነው፡፡ የአገሪቱ የእግር ኳስ ፌደሬሽን በዚህ ታሪካዊ ድል ከፊፋ 35 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ተበርክቶለታል።  የጀርመን ብሄራዊ ቡድን 23 ተጨዋቾች ቃል በተገባላቸው መሰረት በነፍስ ወከፍ 408ሺ ዶላር ይከፍላቸዋል። የጀርመን እግር ኳሷን እዚህ ደረጃ ለመድረስ ከ2000 እ.ኤ.አ በታዳጊ ፕሮጀክት ተስርቶበታል፡፡ በዚህ የለውጥ እንቅስቃሴ የጀርመን እግር ኳስ ፌደሬሽን እና በአገሪቱ ከፍተኛ የስፖርት ባለሙያዎች እና አሰልጣኞች ንቁ ተሳትፎ ነበራቸው፡፡ ከ20 ሺ በላይ የስፖርት መምህሮችና ባለሙያዎች በማሳተፍ የተሰራበት ተእድገት ስትራቴጂ የዓለም ሞዴል መሆን እንደሚገባው የተለያዩ ባለሙያዎች መክረዋል፡፡የጀርመን ክለቦች በታዳጊዎች ላይ የተመሰረተ መዋቅር መያዛቸውም የሊጉ ፉክክር ተመጣጣኝ እና እድገት የሚያሳይ አድርጎታል፡፡ በአውሮፓ ከሚካሄዱ አምስት ታላላቅ ሊጎች የጀርመን ቦንደስ ሊጋ ባለፉት አምስት አመታት በከፍተኛ እድገት ላይ ነው፡፡ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በስታድዬም ተመልካቾች ብዛት፣ በክለቦች ተመጣጣኝ የፉክክር ደረጃ፣ አስተማማኝ ገቢና ጤናማ የፋይናንስ እንቅስቃሴ እንደተምሳሌት የሚታይ ሆኗል፡፡ ከዓለም ዋንጫው በኋላ ይፋ በሆነው ወርሃዊው የፊፋ እግር ኳስ ደረጃ ጀርመን በ1724 ነጥብ አንደኛ ደረጃ ወስዳለች፡፡ ይህ የሚያመለክተው ጀርመን ለሚቀጥሉት አራት አመታት በዚሁ ደረጃ መሪነት ልትቆይ እንደምትችል ነው፡፡ አርጀንቲና በ1606 ነጥብ፤ ሆላንድ በ196 ነጥብ፤እንዲሁም ኮሎምቢያ በ1492 ነጥብ እስከ 4ኛ ያለውን ደረጃ አግኝተዋል፡፡ በአዘጋጀችው ዓለም ዋንጫ 4ኛ የሆነችው ብራዚል በ4 ደረጃዎች በማሽቆልቆል 7ኛ ስትሆን ያለፈው ዓለም ዋንጫአሸናፊ ስፔን በ8 በ7 ደረጃዎች በመውረድ 8ኛ ሆናለች፡፡
 ከ20ኛው ዓለም ዋንጫ ድል በኋላ የጀርመን ማልያ 4 ኮከቦች የሚታተሙበት ይሆናል፡፡ ከ4 ዓመታት በኋላ ዓለም ዋንጫው ለመጀመርያ ጊዜ በምስራቃዊ የአውሮፓ ክፍል ሲካሄድ ጀርመን ካሸነፈች እንደ ብራዚል ባለ አምስት ኮከብ ማልያ ትለብሳለች ተብሎም ተገምቷል፡፡
ተሳታፊዎችን ከ32 ወደ 40 የማሳደግ ሃሳብ ፈጥሯል
20ኛው ዓለም ዋንጫ በተጋባደደ ማግስት የአውሮፓ እግር  ኳስ ማህበር ፕሬዝዳንት የሆኑት ሚሸል ፕላቲኒ ከ4 ዓመት በኋላ ራሽያ በምታስተናግደው 21ኛው ዓለም ዋንጫ የተሳታፊዎችን ቁጥር ከ32 ወደ 40 ማሳደግ እንደሚያስፈልግ መክረዋል፡፡  ተሳታፊዎችን የመጨመሩ አስፈላጊነቱ አንዳንድ አህጉራት በቂ ውክልና ባለማግኘታቸው ነው፡፡ የአፍሪካ እና የኤስያ አህጉራት በጋራ እስከ 100 ፌደሬሽኖችን ቢወክሉም በ9 አገራት የዓለም ዋንጫ ተሳትፎ መያዛቸው ተመጣጣኝ እንዳልሆነ ሚሸል ፕላቲኒ እንደማስረጃ ጠቅሰዋል፡፡ የአውሮፓ አህጉር ከ53 አባልዕ ፌደሬሽኖች የዓለም ዋንጫው ተሳትፎ በ13 ቡድኖች እንደሆነ ይታወቃል፡፡ የፊፋ ፕሬዝዳንት ሴፕ ብላተር የአውሮፓ ቡድኖች በዓለም ዋንጫው ባሳዩት ደካማ ብቃት  ከ13 ቡድን ውክልናቸው ተቀንሶ ለተወሰኑ የአፍሪካ እና የኤስያ ቡድኖች ተጨማሪ እድል እንዲፈጠር ይደረግ የሚል ሃሳብ አስቀድመው አቅርበዋል፡፡ የፊፋ ዋና ፀሃፊ የሆኑት  ዤሮሜ ቫልካ በበኩላቸው የፕላቲኒ ምክር ሊሆን የማይችል ብለው ያጣጣሉት ሲሆን የ21ኛው ዓለም ዋንጫ አዘጋጅ አገር ተወካይ የሆኑት የራሽያ ስፖርት ሚኒስትር ቪታሊ ሙቱኮ ደግሞ በዓለም ዋንጫ ተሳትፎ ላይ  8 ቡድኖችን ጭማሪ ማድረግ አጠያያቂ ነው ብለዋል፡፡ እኝህ የራሽያው ስፖርት ሚኒስትር የተሳታፊ ቡድኖች ብዛት ከ32 ወደ 40 ለማሳደግ መወሰን  በዝግጅታችን ላይ አሉታዊ ተፅእኖ እንደሚፈጥር ይታሰብበት ሲሉ ስጋታቸውን ገልፀዋል፡፡
ሚሸል  ፕላቲኒ ተሳታፊዎች ከ32 ወደ 40 ማደግ እንዳለባቸው  የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ስለሚያምን ለተግባራዊነቱ  ግፊት ማድረጋችን ይቀጥላል ብሏል፡፡ ሃሳቡ ተቀባይነት አግኝቶ በ21ኛው ዓለም ዋንጫ 40 ቡድኖች ከገቡ እያንዳንዱ ምድብ አምስት አገር ሊደለደልበት ይችላል፡፡ ሚሸል ፕላቲኒ ሃሳባቸውን ለእንግሊዙ ታይምስ ጋዜጣ ሲያብራሩ ለ8 ቡድኖች በሚጨመረው አዲስ የተሳትፎ ኮታ ላይ ከአፍሪካ 2፤ ከኤሽያ 2፤ ከሰሜንና መካከለኛው አሜሪካ ሁለት ፤ ከኦሺኒያ 1 እንዲሁም ከአውሮፓ አህጉር 1 ቡድን ተጨማሪ ውክልና ሊያገኙ ይችላሉ፡፡
ባየር ሙኒክና አውሮፓ በገቢ ከፍተኛ ድርሻ አግኝተዋል
በ20ኛው ዓለም ዋንጫ በስፖርት ውድድር ትልቁ ሽልማት ቀርቧል፡፡ በፊፋ የቀረበው 576 ሚሊዮን ዶላር በውድደሩ ታሪክ ሪኮርድ  ሆኖ የተመዘገበ ነው፡፡ ከምድብ ማጣርያ እስከ ዋንጫ በሚገኝ ውጤት መሰረት የገንዘብ ሽልማቱ የሚከፋፈል ሲሆን ለተሳታፊ 32 ቡድኖች ፌደሬሽኖች በቀጥታ የሚሰጥ ነው። ለዋንጫ  አሸናፊው 36.5 ሚሊዮን ዶላር፤ ለሁለተኛ ደረጃ  26.5 ሚሊዮን ዶላር፤ ለሶስተኛ ደረጃ  23.5 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም ለአራተኛ ደረጃ 21.5 ሚሊዮን ዶላር ተበርክቷል፡፡ ሩብ ፍፃሜ የደረሱ 4 ቡድኖች እያንዳንዳቸው 15.5 ሚሊዮን ዶላር፤ ጥሎ ማለፍ ለደረሱ 8 ቡድኖች እያንዳንዳቸው 10.5 ሚሊዮን ዶላርእንዲሁም በምድብ ማጣርያ ለተሳተፉ 16 ቡድኖች እያንዳንዳቸው 19.5 ሚሊዮን ዶላር ያገኛሉ፡፡ በሌሎች የፊፋ ክፍያዎች ተጨዋቾቻቸውን ለብሄራዊ ቡድን ላስመረጡ ክለቦች 70 ሚሊዮን ዶላር፤ ለአዘጋጇ ብራዚል የተሳካ መሰናዶ  20 ሚሊዮን ዶላር እና ለተጨዋቾች የጉዳት ካሳ 100 ሚሊዮን ዶላር የሚሰጥ ይሆናል፡፡ፊፋ በዓለም ዋንጫ በየአገሩ ብሄራዊ ቡድን ለሚሰለፍ ለአንድ ተጨዋች በአንድ ቀን 2800 ዶላር ለክለቡ ከፍሏል፡፡ 14 ተጨዋቾች እስከ ዋንጫ ጨዋታ የደረሱለት የጀርመኑ ባየር ሙኒክ ክለብ ከፍተኛው ክፍያ እንደሚወስድ ተረጋግጧል፡፡ ተጨዋቾቻቸውን ለብሄራዊ ቡድን ላስመረጡ ክለቦች በፊፋ ከተዘጋጀው 70 ሚሊዮን ዶላር ክፍያ የአውሮፓ ታላላቅ ክለቦች 56% ድርሻ አላቸው፡፡ በዓለም ዋንጫ 290 ክለቦች በተጨዋቾቻው ሲሳተፉ 190ዎቹ የአውሮፓ ክለቦች ሲሆኑ ከዓለም ዋንጫው 736 ተጨዋቾች 563 በአውሮፓ ክለቦች የሚጫወቱ ናቸው፡፡

    የደቡብ ጣሊያን ክልል የሆነችው ሲሲሊ ከድሮ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ ዋነኛ መታወቂያዋ ታሪካዊ ቦታዎቿ አልያም በዋና ከተማዋ በናፖሊ ስም የተሰየመው በአንድ ወቅትም የእግር ኳሱ ጣኦት ዲያጎ አርማንዶ ማራዶና ይጫወትበት የነበረው የእግር ኳስ ክለብ ሳይሆን በክልሉ የሚንቀሳቀሰው ማፍያ ነው፡፡
ጣሊያናውያን በካቶሊክ ክርስትና እምነታቸው ዋዛ ፈዛዛ አያውቁም እየተባለ ሲነገርላቸው ቆይቷል። ለሲሲሊው ማፍያ ግን ሃይማኖት እንደ አስፈላጊነቱ የሚታይ ተራ ጉዳይ ነው፡፡ በርካታ ጣሊያናዊ ቄሶች ከካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ቀኖና ውጪ ከሲሲሊ ማፍያ ጋር መነካካት ብቻ ሳይሆን በአባልነትም ጭምር ይንቀሳቀሳሉ እየተባሉ በሰፊው ይታማሉ፡፡ የሮማ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያንም ይህንን ሀሜት እስከ 1993 ዓ.ም ድረስ በይፋ አስተባብላም ሆነ የሲሲሊን ማፍያ አውግዛ አታውቅም፡፡
በ1993 ዓ.ም ግን ሊቀ ጳጳስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ፤ የሲሲሊ ማፍያ በሚፈጽመው የወንጀል ድርጊት የተነሳ የእግዚአብሔር ፍርድ ከመቀበል መቸም ቢሆን እንደማያመልጥ ማስጠንቀቂያቸውን ሰጡ፡፡
ይህን የሰማው የሲሲሊ ማፍያ የሰራው ሀጢያት ይሰረይለት ዘንድ ንስሀ ለመግባትና “ይፍቱኝ አባ!” ለማለት ወደ ቫቲካን አላቀናም፡፡ ይልቁንም ታዛዥና ከተፎ አንጋቾችን ፈንጂ አስታጥቆ ወደ ሮም ከተማ ላካቸው፡፡ በሮም ከተማ የሚገኙ የካቶሊክ ቤተክርስቲያኖችን በማጋየትም ለሊቀ ጳጳስ ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ ማስጠንቀቂያ ምላሹን ሰጠ። ከዚያ ጊዜ ጀምሮ አንድም የሮማ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሊቀጳጳስም ሆነ ሌላ ከፍ ያለ ደረጃና ስልጣን ያለው የቤተክርቲያኗ ቄስ የሲሲሊን ማፍያ ሲያወግዝ ድምፁ ተሰምቶ አያውቅም፡፡
ባለፈው ሳምንት ግን ከወደ ቫቲካን አንድ ፀረ -ማፍያ ድምጽ ተደምጧል፡፡ የሮማ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን መሪ የሆኑት አርጀንቲናዊው ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ ከሲሲሊ የማፍያ ቡድኖች እጅግ አስፈሪ የሆነው የንድራንጊታ ማፍያ ቤተሰብ ዋነኛ መናኸርያ ወደሆነችው የካላብሪያ ከተማ ለስራ ጉዳይ ብቅ ብለው ነበር፡፡ በዚች ከተማ ውስጥ ከጥቂት አመታት በፊት ኒኮላ ካምፓሎንጎ የተባለ የሶስት አመት ሕፃን ከነአያቱና አንድ ሌላ ዘመዱ በንድራንጊታ ማፍያ ቤተሰብ በጥይት ተደብድበው የተገደሉበት ቦታ ላይ ሲደርሱ ቆም አሉና እንዲህ አሉ፤ “የሲሲሊ ማፍያ ከመልካም ነገር ይልቅ ክፉ መስራት የሚያረካው ቡድን ነው፡፡ ይህ የማፍያ ቡድንና ከዚህ የማፍያ ቡድን ጋር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ግንኙነት የሚያደርግ ማናቸውም ሰው ሁሉ ውግዝ ከመአርዮስ!”
በርካታ ጣሊያናውያን የሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስን ግዝት የተቀበሉት በደስታ ነው፡፡ በግዝቱ በፍርሀት ተውጣ እየተንቀጠቀጠች ያለችው ግን በሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ የምትመራው ራሷ የካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ናት፡፡ የሲሲሊ ማፍያ የሚሰጠው ተግባራዊ ምላሽ  ጠንቅቃ ስለምታውቀው ነው፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

የBRICS አገራት አዲስ የልማት ባንክ ሊያቋቁሙ ነው

 እንኳ ብዙ የጓጉለትን ዋንጫ ብሔራዊ ቡድናቸው በደረሰበት አሳፋሪ ሽንፈት የተነሳ ማግኘት ባይችሉም ምርጥ የዓለም ዋንጫ እንዳዘጋጁ የተነገረላቸው የብራዚሏ ፕሬዚዳንት ዴልማ ሩሴፍ ከዓለም ዋንጫው መጠናቀቅ በኋላም ማረፍ አልቻሉም፡፡
ያለፈውን ሳምንት ያሳለፉት ባለፈው ሰኞ የተካሄደውን የBRICS ሀገራት የመሪዎች ጉባኤንና ረቡዕ እለት የተካሄደውን የBRICS የላቲን አሜሪካ ሀገራት የመሪዎች ጉባኤን ለማዘጋጀት ከላይ ታች በመባተል ነበር፡፡
በሰሜናዊ ምስራቅ ብራዚል የባህር ዳርቻ ከተማ በሆነችው በፎርታሊዛ ከተማ ሰኞ እለት በተካሄደው የBRICS ሀገራት ራሺያ፣ ህንድ፣ ቻይናና ደቡብ አፍሪካ የመሪዎች ጉባኤ ላይ መሪዎቹ ከተወያዩባቸው አጀንዳዎች መካከል አንዱና ዋነኛው “በዓለም አቀፉ የኢኮኖሚ መድረክ ከአሜሪካና በምዕራባውያን ከሚመሩ አለም አቀፋዊ የገንዘብ ተቋማት ተፅእኖ እንዴት መላቀቅ እንችላለን?” የሚለው ነበር፡፡
የአምስቱ ሀገራት መሪዎች በጉዳዩ ላይ ለረዥም ሰዓት ከተወያዩ በኋላ የራሳቸው የሆነ የልማት ባንክና የችግር ጊዜ መጠባበቂያ ፈንድ ለማቋቋም ተስማምተዋል፡፡
የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ስምምነቱን በማስመልከት ሲናገሩ፤ “እነዚህን ሁለት የገንዘብ ተቋማት ማቋቋም ከቻልን አሜሪካና የአውሮፓ ተባባሪዎቿ የዓለም ባንክና የዓለም የገንዘብ ድርጅትን በመጠቀም የሚያደርጉትን ተጽዕኖና እጅ ጥምዘዛ በደንብ መቋቋም እንችላለን።” ብለዋል፡፡
አምስቱ የBRICS ሀገራት መሪዎች ከአርጀንቲና፣ ከቺሊ፣ ከኮሎምቢያ፣ ከኢኳዶር፣ ከቬንዙዌላና ከሌሎች የላቲን ሀገራት መሪዎች ጋር ባለፈው ረቡዕ ባደረጉት ጉባኤም ዋነኛው የውይይት አጀንዳ፤ አሜሪካ በላቲን አሜሪካ ያላትን ከፍተኛ ተፅእኖ መቋቋም የሚቻልበት ዘዴ ላይ ያተኮረ ነበር፡፡
በብራዚል ዋና ከተማ ለአንድ ቀን የተካሄደውን ይህን ጉባኤ የተካፈሉ የሀገራት መሪዎች የስብሰባውን ጠቀሜታ የገለፁት ከየሀገሮቻቸው ጥቅምና አመለካከት በመነሳት ነው፡፡
የስብሰባው አዘጋጅና አስተናጋጅዋ የብራዚል ፕሬዚዳንት ዴልማ ሩሴፍ፤ “ጉባኤው ብራዚል ስለ BRICS ሀገራት ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ስለ ላቲን አሜሪካ ሀገራት ትስስርም ጭምር እንደምታስብ ለመሪዎቹ በትክክል ለማስረዳት መልካም አጋጣሚን ፈጥሮላታል፡፡”
በማለት ሲናገሩ፤ የቻይናው ፕሬዚዳንት ዢ ጂንፒንግ በበኩላቸው፤ “ይህ ጉባኤ እንደ አሜሪካ የግል ጓሮ ተደርጎ በሚቆጠረው የላቲን አሜሪካ አህጉር ላይ ቻይና የራሷን ቦታ ለማግኘት ያደረገችውን አዲስ ጥረት በሚገባ ያመላከተ ነው፡፡” ብለዋል፡፡
ይሄው ጉባኤ አዲስ ለተመረጡት የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ፤ ራሳቸውን ለአለም ህዝብ ለማስተዋወቅ አሪፍ መድረክ ሆኖላቸዋል፡፡ የኡክሬን ግዛት የነበረውን የክረሚያን አካባቢ ወደ ራሺያ ግዛት እንዲቀላቀል በማድረጋቸው ከዓለም አቀፍ የፖለቲካ መድረክ ተገልለው ለቆዩት የራሺያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጉባኤው ወደ መድረኩ ብቅ እንዲሉና ከተለያዩ ሀገራት መሪዎች ጋር እንዲቀላቀሉ እድር ፈጥሮላቸዋል፡፡
የላቲን አሜሪካ ሀገራት መሪዎች ደግሞ ከBRICS ሀገራት ጋር ጠንካራ ግንኙነት መፍጠራቸው እነዚሁ ሀገራት ከሚያቋቁሙት አዲሱ የልማት ባንክ ተጠቃሚ መሆን እንችላለን የሚል አዲስ ተስፋ መሰነቅ አስችሏቸዋል፡፡
የBRICS ሀገራት የሚያቋቁሙት አዲሱ የልማት ባንክ የሚመሰረተው በ50 ቢሊዮን ዶላር ካፒታል ሲሆን ይሄው ካፒታል ወደ 100 ቢሊዮን ዲላር ከፍ እንዲል ይደረጋል ተብሏል፡፡ የአደጋ ጊዜ መጠባበቂያ ፈንድ ካፒታል ደግሞ 100 ቢሊዮን ዶላር ይሆናል። የዚህ ባንክ ዋና ጽህፈት ቤትም በቻይናዋ ሻንሀይ ከተማ እንደሚሆን ታውቋል፡፡ 

Published in ከአለም ዙሪያ
Saturday, 19 July 2014 12:51

“ውረድ ወይም ፍረድ!”

ኢትዮጵያውያን በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚና በማህበራዊ ኑሮአቸው የተጠቁና የተገፉ ሲመስላቸው ከሌላ ከማንኛውም አካል ይልቅ ስሞታቸውን የሚያቀርቡት ለአምላካቸው ነው። ጥቃታቸውንና መገፋታቸውን አይቶ መልስ እንዲሰጣቸው አምላካቸውን “ውረድ ወይም ፍረድ!” እያሉ ይማፀኑታል፡፡ አንዳንዴም ያዙታል፡፡
ልክ እንደ ኢትዮጵያዊያኑ ሁሉ በፍርደ ገምድል ኢ-ፍትሀዊ ውሳኔ እድሜ ልኩን በወህኒ እንዲማቅቅ የተፈረደበት የሰሜን ካሮላይና ግዛት ነዋሪው አሜሪካዊው ዳሪል አንቶኒ ሆዋርድም ያጋጠመውን ከፍተኛ የፍትህ መጓደል አይቶ መፍትሄ እንዲሰጠው “ውረድ ወይም ፍረድ!” ብሎ ኤሎሄ ያለው ለአምላኩ ብቻ ነው፡፡
በ1991 ዓ.ም በዱርሀም የመኖሪያ አካባቢ ነዋሪ በነበረችው ዶሪስ ዋሽንግተንና የ13 ዓመት ሴት ልጇ ኒሾንዳ ግድያ እጁ አለበት በሚል ያለ በቂ ማስረጃ በ1995 ዓ.ም የእድሜ ልክ እስራት የተፈረደበት ዳሪል ሆዋርድ ያለፉትን 19 ዓመታት ለአንድም ቀን ሳይሰለችና ፈጽሞ ተስፋ ሳይቆርጥ አምላኩን “ውረድ ወይም ፍረድ!” እያለ በመማፀን አሳልፏል፡፡
“ውረድ ወይም ፍረድ!” ተብሎ ተማጽኖ የቀ    ረበለት አምላክ አልወረደም፡፡ ግን ፍርዱን ፈረደለት። የመጀመሪያውን የፍርድ ውሳኔና የቀረበለትን አዲስ ማስረጃ የመረመረው የሰሜን ካሮላይና ግዛት የይግባኝ ፍርድ ቤት፤ ዳሪል ሆዋርድ የእድሜ ልክ እስራት የተፈረደበት ጨርሶ ባልፈፀመው ወንጀልና ምንም አይነት በቂ አሳማኝ ማስረጃ ሳይቀርብበት ነው በማለት ባለፈው ማክሰኞ በነፃ አሰናብቶታል፡፡
የግዛቲቱ የይግባኝ ፍርድ ቤት ዋና ዳኛ የሆኑት ኦርላንዶ ኸድሰን፤ የዳሪል ሆዋርድን የመጀመሪያ ፍርድ አስመልክተው ሲናገሩ፤ “አቃቤ ህጎቹ ማስረጃዎቹን በሙሉ ደብቀዋቸዋል፡፡ ፖሊሱም የዳኞች ጉባኤውን አሳስቷል፤ ይህ በህግ ሙያ ባሳለፍኩት 34 ዓመታት ውስጥ አጋጥሞኝ የማያውቅ እጅግ አሳፋሪና ዘግናኝ የፍትህ ስህተት ነው፡፡” ብለዋል፡፡
የዳሪል ሆዋርድ ጉዳይ ዳግመኛ እንዲታይ ለይግባኝ ፍርድ ቤት ያመለከቱትና እውነተኛውን ወንጀለኛ የሚያሳይ የዲኤንኤና ሌሎች ማስረጃዎችን በማሰባሰብ በነፃ ጥብቅና ቆመው የተሟገቱለት “Innocence Project” የተባለ ምግባር ሠናይ የህግ ባለሙያዎች ድርጅት ጠበቆች ናቸው፡፡
የይግባኝ ፍርድ ቤቱን ውሳኔ ለዳሪል ሆዋርድ በስልክ ያበሰረችው ጠበቃው ሲማ ሲያይፊ፤ “ለመሆኑ በነፃ መለቀቁን መጀመሪያ ስትነግሪው ዳሪል ሆዋርድ ምን አለሽ?” ተብላ ሰትጠየቅ የሰጠችው መልስ “ወህኒ ቤት ሄጄ በአካል በማግኘት ዜናውን ልነግረው አስቤ ነበር፡፡ ነገር ግን ጨርሶ አላስችል አለኝና ስልክ ደውየ ነገርኩት፡፡ ልክ ነገሩ እውነት መሆኑን ሳረጋግጥለት በከፍተኛ የደስታ ሲቃ “አምላክ ፈረደ! የእውነት አምላክ ፈረደ!” አለኝ፡፡ ዳሪል ሆዋርድ ይህንን ፍርድ ለመስማት ለ19 ዓመታት በትእግስት ጠብቋል፡፡ እሱ ፈጽሞ ተስፋ የማይቆርጥ ሰው ነው፡፡” የሚል ነው፡፡
ዳሪል ሆዋርድ በጥቁርነታቸው የተነሳ ከፍተኛ የፍትህ መጓደል ከተፈፀመባቸውና የዘረኝነት ሰለባ ከሆኑ በርካታ አሜሪካውያን አንዱ ነው፡፡ በ1995 ዓ.ም ያለ ትክክለኛና በቂ ማስረጃ የእድሜ ልክ እስራት የፈረዱበት ዳኛ ማይክል ኒፎንግ በጥቁር፣ ጠል አቋማቸው ባለ ሪከርድ ናቸው፡፡ ተከሳሹ ጥቁር ብቻ ይሁን እንጂ ስለሚቀርብበት ማስረጃ ግድ የላቸውም፡፡ ፍርዳቸውም ፍርደ ገምድል ነው፡፡
የሰሜን ካሮላይና ግዛት የፍትህ ቢሮ፤ እኒህን ዘረኛ ፍርደ ገምድል ዳኛ እንደነገሩ እያስታመመ እስከ 2007 ዓ.ም ድረስ ታግሷቸው ነበር፡፡ በ2007 ዓ.ም በአስገድዶ መድፈር ወንጀል በሀሰት ተከሰው በቀረቡት የዱክ ዩኒቨርሲቲ ጥቁር ተማሪዎች ላይ ያለ በቂና ትክለለኛ ማስረጃ ከባድ እስር ቅጣት ካስተላለፉ በኋላ ግን በዝምታ ሊታለፉ አልቻሉም። የዳኝነትና የጥብቅና ፈቃዳቸውን በመንጠቅ በሰሜን ካሮላይና ግዛት የፍትህ አደባባይ ዳግመኛ ዝር እንዳይሉ አባሯቸዋል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

በዕውቁ ጋዜጠኛ፣ ደራሲና የታሪክ ተመራማሪ ጳውሎስ ኞኞ የሕይወት ታሪክ ዙርያ የሚያጠነጥን አዲስ መፅሐፍ ሰሞኑን በገበያ ላይ ዋለ፡፡
ጳውሎስ ከዚህ ዓለም በሞት ከተለየ 22 ዓመታት በኋላ በጋዜጠኛ ደረጀ ትዕዛዙ የተዘጋጀው ይኸው መጽሐፍ፤ በ308 ገፆች የተቀነበበ ሲሆነ በዘጠኝ ምዕራፎች የተከፋፈለና በበርካታ መረጃዎች የተጠናቀረ ነው፡፡
ከአራተኛ ክፍል የዘለለ የመደበኛ ትምህርት ያልነበረው ጳውሎስ፤ ዝነኝነት ለመቀዳጀት ያበቁትን በርካታ ስራዎች ለማከናወን መቻሉ የህይወት ታሪኩን ለማሰናዳት እንዳነሳሳው አዘጋጁ አስረድቷል፡፡ በአርቲስቲክ ማተሚያ ቤት የታተመው መጽሐፉ፤ በ84 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡  

“የአዲስ አበባ ጉዶች” እና “ኢትዮጵያን ማን ይታደጋት” በሚሉት መፅሀፎቹ የሚታወቀው ጋዜጠኛና ደራሲ አቤል አለማየሁ፤ “የእኛ ሰው ገመና” የተሰኘውን ሦስተኛ መፅሀፉን በሳምንቱ መገባደጃ ላይ ለንባብ አብቅቷል፡፡ የተደበቁ እውነቶችን ምፀታዊ ወጎች፣ ማህበራዊና ወሲባዊ ጉዳዮችን የሚዳስሰው መፅሀፉ፤ በተለይም በድንግልና ንግድ፣ በሴት ሰዶማውያውን፣ በልቅ ወሲብና በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵዊያንን አስገራሚ ገመናዎች በስፋት ያስቃኛል፡፡ ለአፍሪካ ዋንጫ ወደ ደቡብ አፍሪካ ተጉዞ የነበረው አቤል፤ በቆይታው የታዘባቸውን የሀበሻ ልጆች ገመና ዋና የመፅሃፉ ትኩረት ማድረጉን ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡
በ208 ገፆች የተቀነበበውና በርካታ ማህበራዊ ርዕሰ ጉዳዮችን የሚዳስሰው መፅሀፉ፤ በ49 ብር ከ65 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡

Page 4 of 16