ትናንት በተከፈተው የሞንታና ፎልክ ፌስቲቫል ፈንዲቃ የባህል ቡድን ኢትዮጵያን በመወከል እንደሚሳተፍ ተገለፀ፡፡ ከ200 አገራት የተውጣጡ የሙዚቃ ቡድኖችና የፋሽን ባለሙያዎች የሚሳተፉበት ዓለም አቀፉ የሙዚቃ ፌስቲቫል እስከ 31 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ የንግድ ስራዎች የሚንቀሳቀስበትና ከ16ሺ በላይ ጎብኝዎች የሚገኙበት ነው፡፡ ፈንዲቃ የኢትዮጵያ አዝማሪ ባንድ እና የባህል ውዝዋዜ ቡድን ሲሆን ስድስት ሙዚቀኞች፤ ሁለት ተወዛወዦች እና አንድ ድምፃዊን በማቀፍ በሞንታና ፎልክ የሙዚቃ ፌስቲቫል በመሳተፍ የአገር ባህልን በማስተዋወቅ ከፍተኛ ትኩረት ያገኛል ተብሏል፡፡ ፈንዲቃ የባህል ቡድን ከአምስት ዓመት በፊት በተወዛዋዥነቱና በባህል አምባሳደርነቱ በሚታወቀው አርቲስት መላኩ በላይ እንደተመሰረተ ይታወቃል፡፡

አዳዲስና ነባር የልጆች ተረቶች የተካተቱበት “የልጆች ዓለም” መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ ዝግጅትና ቅንብሩ በመብራቱ ካሳ የተሰራው መጽሐፍ በሥዕሎች የታጀበ ሆኖ 85 ገፆች አሉት፡፡ በነጭ ሳር ማተሚያ ድርጅት የታተመው “ከልጆች ዓለም” በ25 ብር ከ30 ለገበያ ቀርቧል፡፡

በአለን ሌከን ተፅፎ አባተ መንግሥቱ የተረጐመው “ስኬታማ የጊዜ አጠቃቀም” እየተሸጠ ነው፡፡ በውጤታማ የጊዜ አጠቃቀም ዙርያ የተፃፈው መፅሐፍ ኤችኬ ፐብሊሺንግ የታተመ ሲሆን ዋጋው 25 ብር ከ35 ነው፡፡የመጽሐፉን የአርትኦት ስራ ደራሲና ሃያሲ መስፍን ሃብተማርያም ነው የሰራው፡፡ ይህ በዚህ እንዳለ የሮቢን ሻርማ “The Monk Who Sold His Ferrari” በብርሃኑ በላቸው “ራስን ማወቅ” በሚል ርዕስ ተተርጉሞ ለገበያ የበቃ ሲሆን በ35 ብርም እየተሸጠ ነው፡፡ በፋርኢስት ትሬዲንግ የታተመው መፅሐፉ፤ 176 ገፆች አሉት፡፡ መፅሐፉን መገናኛ አካባቢ የሚገኘው ዩኒቲ መፃህፍት መደብር እንሚያከፋፍል ታውቋል፡፡

በወይንሸት መርከቡ የተደረሱ አምስት አጫጭር ልቦለዶች የተካተቱበት “እኔና ቄስ ገንዘቤ” የአጫጭር ልቦለዶች መድበል ለንባብ በቃ፡፡ በመፅሐፉ “እኔና ቄስ ገንዘቤ” ባለ አራት ክፍል አጭር ልቦለድ እንዲሁም “ማትሪክ”፣ “አቢይ እና አባይ”፣ “ኮሌጅ” እና “ይድረስ ለፈጣሪ” የተሰኙ ሌሎች አጫጭር ልቦለዶች ተካተውበታል፡፡ 118 ገፅ ያለው መፅሐፉ ባናዊ ማተሚያ ቤት የታተመ ሲሆን ዋጋው ለሀገር ውስጥ 25 ብር፣ ለውጭ ሀገራት 10 ዶላር ነው፡፡ በሰሎሞን ታደሰ የተደረሱ ወጐችና እውነተኛ ታሪኮች የተካተቱበት “የሸገር ወጐች እና እውነተኛ ታሪኮች” መፅሐፍ እንዲሁ ለንባብ በቅቷል፡፡ በመፅሐፉ “የሸገር ወጐች”፣ “መጣንላችሁ ማሳጆች”፣ “የጨለሙ ታሪኮች በዱባይ” እና ሌሎች ታሪኮች ተካተዋል፡፡ ደራሲው ካሁን በፊት “ቦሌ ፒኮክ ጋ ጠብቂኝ” የተሰኘ መፅሐፍ ለንባብ አብቅቷል፡፡ “የሸገር ወጐች” በ39.50 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

በሙዚቃው ንጉስ ማይክል ጃክሰን አሟሟት ላይ በተመሰረተ ክስ የተጀመረው የፍርድ ሂደት 10ኛ ሳምንቱን ሲይዝ ሁኔታዎች እየተወሳሰቡ መምጣታቸውን ዘገባዎች አመለከቱ፡፡ ታዋቂው የኮንሰርት አዘጋጅ ኤኢጂ ላይቭ ለአሟሟቱ ተጠያቂ መሆን አለበት በሚል የማይክል ካትሪን ጃክሰን እና ቤተሰባቸው ክስ እንደመሰረቱ ሲታወቅ፤ በክሱ የ40 ቢሊዮን ዶላር ካሳ የከፈለን በሚል እየተሟገቱ ናቸው፡፡ ማይክል ጃክሰን ከአምስት ዓመት በፊት ከመጠኑ ያለፈ መድሃኒት በመውሰድ ለድንገተኛ ሞት መብቃቱ የሚታወስ ሲሆን የተጠየቀው ካሳ አርቲስቱ በ50 ዓመቱ እድሜው ህይወቱ ባያልፍ ኖሮ በኮንሰርት ስራዎች እና በአልበም ሽያጭ ሊያገኝ የሚችለው ገቢን በማስላት የተተመነ ነው፡፡ የግሉ ሃኪም የነበሩት ዶክተር ኮናርድ ሙራይ ለሞቱ መንስኤ የሆነ መድሃኒት ያለጥንቃቄ ሰጥተዋል በሚል ክስ ተጠያቂ መደረጋቸው ይታወቃል፡፡ አሁን በተጀመረው የፍርድ ክርክር ደግሞ የኮንሰርት አዘጋጁ ኤኢጂ ላይቭ ታላቁን ሙዚቀኛ አላግባብ ትኩረት በመንፈግ ከሞት አደጋው ሳይታደጉ ቀርተዋል በሚል ተከስሰዋል፡፡ የኤኢጂ ጠበቃዎች ማይክል ጃክሰን ለሞት የተዳረገው ራሱ በቀጠረው እና በወር እስከ 150ሺ ዶላር በሚከፍለው የግሉ ሃኪም ስህተት እንጂ ከሚያቀርበው ዓለም አቀፍ ኮንሰርት በተያያዘ አለመሆኑን በመግለፅ የክስ መከላከያቸውን አቅርበዋል፡፡

ኤኢጂ ላይቭ የማይክል የግል ሀኪም የነበሩትን ዶክተር ኮናርድ ሙራይ አልቀጠርኩም ብሎ ከመካዱም በላይ ለሞቱ ምን ሃላፊነት የለብኝም ይላል፡፡የማይክል ቤተሰብ በጉዳዩ ላይ 97 ምስክሮችን እንዲሁም ኤኢጂ ላይቭ ደግሞ 113 ምስክሮችን ለክስ መከላከያው በማቅረብ ለወራት በጉዳዩ ላይ በመሟገት ይቀጥላሉ፡፡ በሌላ ዜና ማይክል ጃክሰን በሞቱ ማግስት በ500 ሚሊዮን ዶላር እዳ ተይዞ እንደነበር ያስታወሰው ሴሌብሪቲኔይዎርዝ ከዚህ እዳው ሙሉለሙሉ ነፃ መውጣቱን አስታውቋል፡፡ የማይክል ጃክሰን ሃብት ንብረትን ለመሰብሰብ ቤተሰቡ ለጠበቆች እስከ 13.6 ሚሊዮን ዶላር መክፈላቸውን ያወሳው ሴለብሪቲ ኔትዎርዝ የሃብት መጠኑ 600 ሚሊዮን ዶላር እንደሚደርስ አመልክቷል፡፡ ማይክል ጃክሰን በኑዛዜው ከሃብት ንብረቱ 40 በመቶውን ለልጆቹ፤ 40 በመቶውን ለእናቱ እና ቀሪውን 20 በመቶ ለበጎ አድራጎት መለገሱ ሲታወቅ እናቱ ካተሪን ጃክሰን ከመየርሳቸውን ድርሻ ልጆቹ እንዲወርሱ መናዘዙን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ታዋቂው ራፐር 50 ሴንት በቀድሞ ፍቅረኛው ላይ አድርሷል በተባለ ጥቃት ሊከሰስ ነው፡፡ ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘ የአምስት አመት እስርና የ46ሺ ዶላር ካሳ እንዲከፍል እንደሚወሰንበት የቢልቦርድ ዘገባ አመልክቷል፡፡ 50 ሴንት ከሁለት ሳምንት በፊት ወደ ቀድሞ ፍቅረኛው የኮንዶሚኒዬም መኖርያ በመሄድ ጥቃት ማድረሱ ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል ከፈፀመው ፆታዊ ጥቃት ጋር በትችት መወጠሩ ሳያንሰው ራፐሩ በስልክና በፅሁፍ መልዕክት የ16 ዓመት ልጁን በማስፈራራቱም እየተብጠለጠለ ነው፡፡ ራፐሩ ከታዳጊ ልጁ ጋር በስልክ ባደረገው ንግግር “የእናትህ ልጅ እንጂ የእኔ አይደለህም፡፡ ገና የደም ምርመራ ሁሉ አደርጋለሁ፡፡ እንደ እናትህ እና እንደ ቤተሰብህ ከእኔ የምትፈልገው ስጦታ ብቻ ነው፡፡ ከእንግዲህ ግን ምንም እንዳትጠብቅ፡፡ ስልኬን ሰርዘው፡፡ ሁለተኛም እንዳትደውልልኝ” ብሎታል፡፡

ቢልቦርድ መፅሄት እንደዘገበው፤ ራፐሩ በቀድሞ ፍቅረኛው እና በልጁ ላይ የፈፀማቸው ተግባራት ገፅታውን እያበላሸበት ነው፡፡ በሌላ በኩል ፊፍቲ ሴንት ከሙዚቃው ባሻገር በተሰማራበት ንግድ እጅግ ትርፋማ እየሆነ መምጣቱን ያመለከተው ሂፖፕ ኒውስ፤ በ260 ሚሊዮን ዶላር ከአምስቱ የዓለም ሃብታም ራፐሮች አንዱ ሊሆን እንደበቃ ጠቁሟል፡፡ ለ50 ሴንት ሃብት ማደግ በዋናነት “ቪታሚን ዎተር” በተባለው የውሃ ምርት አምራች ኩባንያ ያዋለው ኢንቨስትመንት ትርፋማነት መሆኑን የጠቀሰው ዘገባው፤ ‹ጂ ዩኒት› በተባለው የፋሽንና የሙዚቃ ኩባንያው እንዲሁም በፊልም ስቱድዮው እና በተለያዩ የማስታወቂያ ስራዎችም የተወጣለት ነጋዴ መሆኑን አብራርቷል፡፡

• እናቶች ለእርግዝና ክትትል ወደጤና ተቋም በሚቀርቡበት ጊዜ ተመርምረው ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ከሆኑ ወዲያውኑ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መድሀኒቱን አንዲጀምሩ ይደረጋል፡፡ • ኤችአይቪ ቫይረስ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ይበልጥ የሚመረጠው እናቶቹ የእድሜ ልክ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ ነው፡፡ ኤችአይቪ ቫይረስ ከእናት ወደልጅ እንዳይተለሰለፍ ለመታደግ ሲባል የአለምአቀፉ የጤና ድርጅትን ጨምሮ በየአህጉሩ ያሉ ብሔራዊ ተቋማት እና ሌሎች አለምአቀፋዊ ድርጅቶችን ጨምሮ የተለያዩ ጥረቶች መደረግ ከጀመረ ሰንበትበት ብሎአል፡፡ የሚወለዱ ሕጻናት ከእናቶ ቻቸው የኤችአይቪ ቫይረስን እንዳይወስዱ ለማድረግ የሚያስችሉ ግኝ ቶች እና አሰራሮች በመዘርጋታቸው ከቫይረሱ ነጻ የሆኑ ሕጻናትን ማዋለድ ተችሎአል፡፡ ከእናት ወደ ልጅ የሚተላለፈው የቫይረሱ ስርጭት በእርግዝና ፣በምጥ ፣በመው ለድ ወይንም ጡት በማጥባት ሲሆን ስርጭቱም ከ25-45 % የሰፋ ነው፡፡

የኤችአይቪ ቫይረስን ስርጭት ለመግታት አስቸኩዋይ እቅድ የማወጣት ፕሮግራም ወይንም ደግሞ pepfar (ፔፕፋር) ተብሎ የሚጠራው ሰፊ ፕሮግራም ባወጣው መረጃ መሰረት የዛሬ አራት አመት ገደማ በአለም ላይ ወደ 390,000- (ሶስት መቶ ዘጠና ሺህ) የሚጠጉ ህጻናት ከቫይረሱ ጋር ተወል ደዋል፡፡ ከእነዚህ ህጻናት ውስጥ 90 % የሚ ሆኑት ከሰሃራ በታች ያሉ ሀገራትን ጨምሮ በ22/ ሀገሮች ውስጥ የተወለዱ ናቸው፡፡ ባደጉት ሀገሮች ውስጥ ከእናት ወደ ልጅ የሚተላለፈው የቫይረሱ ስርጭት ሙሉ ለሙሉ ተገትቶአል ማለት የሚያስችለው የ pepfar ጥናት በእርግዝና ጊዜ የጸረ ኤች አይቪ መድሀኒትን ትክለኛ የሆነ አጠቃቀምና ከወሊድ በሁዋላ ጡት ባለማጥባት ቀጥተኛ የሆነውን የቫይረሱን ስርጭት እስከ 5 % ድረስ መቀነስ ይቻላል ብሎአል፡፡ pepfar የዛሬ ሶስት አመት ባደረገው ዘመቻ መሰረት 9.8/ ሚሊዮን የሚሆኑ እር ጉዝ ሴቶች የኤችአይቪ ምርመራ እንዲያደርጉ ከእነዚያ ውስጥ 660,000/ያህሉ ቫይረሱ በደማ ቸው ተገኝቶ ነበር፡፡ እነዚህ እናቶች ቫይረሱን ወደልጆቻቸው እንዳያስተላልፉ ሲባል ART የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት እንዲወስዱ ተደርጎአል፡፡

ይህ በመሆኑ ከ200,000/ (ሁለት መቶ ሺህ .. በላይ የሆኑ ሕጻናት ከኤችአይቪ ነጻ ሆነው እንዲወለዱ እድሉ ተፈጥሮአል፡፡ ከእናታቸው በቀጥታ ቫይረሱን የተቀበሉ ሕጻናት በሕይወት የሚቆዩት ቢበዛ እስከ ሁለት አመት እድሜያቸው ድረስ ነው፡፡ ከኤድስ ነጻ የሆነ ትውልድን ለማፍራት የሚደረገው እርብርብ አ.ኤ.አ በ2015/ ለታቀደው የሚሊኒየም ግብ 90% የሚሆነውን ከእናት ወደልጅ የሚተላለፈውን የቫይረሱን ስርጭት ይገታል የሚል ተስፋ አለ፡፡ ሕጻናት የኤችአይቪ ቫይረስን ከእናታቸው እንዳይወርሱ ከሚያስችለው አለምአቀ ፋዊ ጥረት መካከል እርጉዝ የሆኑ እናቶች ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ከተገኘ በቀጥታ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒቱን እንዲወስዱ ማድረግ ይገኝበታል፡፡ ይህም በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን በተግባር ላይ እንዲውል የሚያስችል አሰራር የተዘረጋ ሲሆን ይህንን በሚመለከት ማብራሪያ እንዲሰጡን የጋበዝነው ዶ/ር ታደሰ ከተማ በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የእናቶች ጤና አማካሪ ናቸው፡፡ ዶ/ር ታደሰ እንደሚገልጹት በኢትዮጵያ ላለፉት አስር አመታት በላይ ኤችአይቪ ከእናቶች ወደ ልጆች እንዳይተላለፍ ለማድረግ የሚያስችል አሰራር በተግባር ውሎአል፡፡ አሰራሩን አስተማማኝ በሆነ መንገድ ለመለወጥና ከኤችአይቪ ነጻ የሆነ ትውልድ ለማፍራት እንዲያስችል የተለየ አገልግሎት በየጤና ተቋማቱ እንዲሰጥ በመደረግ ላይ ነው፡፡ ይህ አገልግሎትም ከአሁን ቀደም ቫይረሱ ያለባቸውን እርጉዝ ሴቶች በመለየት ለአጭር ጊዜ የሚቆይ ጸረኤችአይቪ መድሀኒት ይሰጥ የነበረ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ግን የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ለእድሜልክ እንዲሆን ተወስኖአል፡፡

የዚህ አላማም ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ከማድረግ ባሻገር እናት ከኤችአይቪ ጋር በተያያዘ ሌሎች ሕመሞችን እንዳትታመም እና የእራስዋን ጤንነት ለመጠበቅ እንዲያስችላት ነው፡፡ስለዚህም እናቶች ለእርግዝና ክትትል ወደጤና ተቋም በሚቀርቡበት ጊዜ ተመርምረው ፖዘቲቭ የሆኑት ወዲያውኑ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መድሀኒቱን አንዲጀምሩ ይደረጋል፡፡ እርጉዝ ሴቶችም ሆኑ ሌሎች ሰዎች በደማቸው ኤችአይቪ ቫይረስ የሚገኝ ከሆነ የሰውነታቸው የመከላል አቅም እና በሰዎቹ ላይ የተከሰተውን የተለያየ ሕመም መሰረት በማድረግ ቫይረሱ ያለበት ደረጃ ከታየ በሁዋላ ጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት መውሰድ የሚገባቸውንና የማይገባቸውን በመለየት መድሀኒቱ ይሰጥ እንደነበር ይታወሳል፡፡ አሁን ግን እናቶቹ የሰውነት የመከላከል አቅማቸው ያለበት ደረጃ በምርመራ እንዲታወቅ የሚደረግ ሲሆን ያ የሚደረገው ግን ፀረ ኤችአይቪ መድሀኒቱን ለመጀመር ሳይሆን የጤንነታቸው ሁኔታ ያለበትን ደረጃ ለማወቅ እና ክትትሉን ለማድረግ እንዲያስችል ሲባል ነው፡፡ ፀረ ኤችአ ይቪ መድሀኒትን ቀድሞ መጀመር ከኤችአይቪ ጋር ተያይዘው የሚመጡ የተለያዩ በሽታዎችን እንዳይኖሩ ከማድረግ በተጨማሪ እናቶቹ ለረጅም ጊዜ ጤንነታቸው ተጠብቆ እንዲኖሩ ፣የሚወልዱዋቸው ሕጻናትም ከቫይረሱ ነጻ ሆነው እንዲወለዱ ይረዳቸዋል፡፡ ዶ/ር ታደሰ ከተማ እንደገለጹት እናቶች የእድሜ ልክ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያደርገው አሰራር ኤችአይቪን በተመለከተ ልዩ ትኩረት ያስፈልጋቸዋል በተባሉ 22/ ሀገራት ተሞክሮ ውጤት ያስመዘገበ ሲሆን በተለይም ማላዊ የተሳካ ልምድ ያገኘችበት ነው፡፡

የአለም የጤና ድርጅት ለእናቶች ጤና ተገቢው እና ትክክለኛው ነው በሚል እንዲተገበር ብዙ አገራትን እያማከረ እና አቅጣጫን እያስያዘ ያለበት አሰራር በመሆኑ በኢትዮጵያም ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል፡፡ ኤችአይቪ ቫይረስ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ የሚሰጠው አገልግሎት በደረጃ ሊከፋፈል የሚችል ነው፡፡ •በእርግዝና ወቅት እናቶች የእርግዝና ክትትል እንዲያደርጉ ማድረግ፣ •የኤችአይቪ የምክርና የምርመራ አገልግሎት መስጠት፣ •እናቶች በጤና ተቋማት እንዲወልዱ ማድረግ፣ •ከኤችአይቪ ፖዘቲቭ እናቶች የተወለዱት ሕጻናት ክትትል እንዲያደርጉ ማድረግ፣ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ እናቶች የእርግዝና ክትትል የማድረጋቸው ሁኔታ ቀደም ካሉት ጊዜያት የተሸሻለ ደረጃ ላይ የሚገኝ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ወደ 20 % የነበረው የእር ግዝና ክትትል ዛሬ ወደ 80% ደርሶአል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ከ35 -45 % የማያንሱ እናቶች የኤችአይቪ የምክርና የምርመራ አገልግሎት ያገኛሉ፡፡ በአገሪቱ በአጠቃላይ ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ይሆናሉ ተብሎ ከሚገመቱት ወደ 34000/ እናቶች ውስጥ 42 % የሚሆኑት ቫይረሱ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡

ከተወለዱት ልጆችም የህክምና ክትትል እየተደረገላቸው የሚገኙ የመኖራቸውን ያህል በተለይም ቤተሰቦች ከተወሰነ ጊዜ በሁዋላ የሚያቋርጡ በመሆኑ እንደ አንድ ችግር የሚታይ ነው፡፡ አንዳንድ ኤችአይቪ ፖዘቲቭ የሆኑ እናቶችም የህክምና ክትትላቸውን በትክክል ሳያቋርጡ የማይከታተሉ በመሆኑ በዚህ ረገድ ገና ብዙ መሰራት የሚጠበቅበት ሆኖ ተገኝቶአል፡፡ ምንም እንኩዋን ከነበረበት ሁኔታ የተሸሻለ ነገር ይታያል ቢባልም በአጠቃላይ አላማው ከቫይረሱ ነጻ የሆኑ ልጆችን ማዋለድ ሲሆን ይህንን ግን በትክክል ለማወቅ የሚያስችል አካሄድ እስከአሁን ማግኘት አልተቻለም፡፡ እ.ኤ.አ በ2011/ የተሰራ አገር አቀፍ ጥናት እንደሚጠቁመው በኢትዮጵያ ውስጥ ቀደም ሲል የነበረው የቫይረስ ስርጭት እየቀነሰ መምጣቱን ያመላክታል፡፡

በዚህም ጥናት መሰረት ቀደም ሲል ወደ 3% የነበረው አሁን 1.5% በሚል ሊጠቀስ እንደሚችል ጥናቱ ያሳያል፡፡ ቀደም ሲል ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ይሆናሉ ተብለው የሚገመቱ እናቶች ቁጥር ወደ 80,000/ እና 90,000/ ገደማ የነበረ ሲሆን በዚህ ጥናት የታየው ግን ከ34,000 ብዙም የማይበልጡ እናቶች ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ይሆናሉ የሚል ግምት አለው፡፡ ይህም የግንዛቤ ማስጨበጥን ስራ እና በተለያዩ ተቋማት የሚሰሩ ስራዎችን ውጤታማ አካሄድ የሚያ ሳይ ሲሆን እነዚህ አካላት ወደፊትም ብዙ እንዲሰሩ የሚጠበቅበት ሁኔታ መኖሩ ግልጽ ነው ብለዋል ዶ/ር ታደሰ ከተማ፡፡ በእርግዝና ክትትል ወቅት ኤችአይቪ በደማቸወ ውስጥ የተገኘባቸው እናቶች ቁጥር እና ጸረ ኤችአይቪ መድሀኒትን ተጠቃሚ የሆኑት ቁጥር በፊት ከነበረበት 25% አሁን ወደ 42% ደርሶአል፡፡ ስለዚህ እናቶች ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ከተገኝ የእድሜ ልክ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ ይሁኑ ሲባል ቫይረሱ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይ ተላለፍ እና እናቶችም ጤንነታቸው በተጠበቀ ሁኔታ ሕይወታቸውን እንዲቀጥሉ ለማስቻል መሆኑን ሁሉም ሊረዳው ይገባል፡፡

ኢትዮጵያ በሚቀጥሉት ሶስት አመታት ውስጥ ኤችአይቪ ከእናት ወደ ልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ ወይም መተላለፉን ለማጥፋት እቅድ ይዘው እየሰሩ ካሉ አገሮች ውስጥ አንዱዋ ነች፡፡ ስለዚህም ይህንን አለማ እውን ከማድረግ አንጻር ይህ የጸረ ኤች አይቪ መድሀኒት ለሁሉም ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ለሆኑ እርጉዝ ሴቶች በዘለቄታዊ መንገድ መስጠት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ዶ/ር ታደሰ ከተማ በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የእናቶች ጤና አማካሪ እንዳብራሩት፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

ከአስራ አምስት ዓመት በፊት ወደ ሙዚቃ ሙያ የገባው ድምፃዊ ሸዋንዳኝ ኃይሉ፣ ባለፈው ሳምንት “ስጦታሽ” የተሰኘውን ሁለተኛ አልበሙን ለአድማጭ ጆሮ አድርሷል፡፡ “ስቅ አለኝ” በተባለው የመጀመርያ ስራው ከህዝብ ጋር የተዋወቀው አርቲስቱ፤ እ.ኤ.አ በ2004 ዓ.ም በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው “ኮራ” የሙዚቃ ውድድር ላይ እጩ ሆኖ ለመመረጥ በቅቷል። የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው በአዲሱ አልበሙና በሙዚቃ ህይወቱ ዙሪያ አነጋግራዋለች፡፡

ስቱዲዮ በሄድኩ ቁጥር መብራት እየጠፋ ያስቸግረን ነበር
ስታይላችን ቢቀራረብም እኔም ራሴን ነኝ፣ ቴዲም ራሱን ነው
ፎቶውን ያነሳኝ አንቶኒዮ ፊዮሬቴ ነው፤ ተሰቅሎ ሳየው ደስ ብሎኛል

 አዲሱ አልበምህ ገበያው እንዴት ነው? 

የአገር ውስጥ ሽያጩን በተመለከተ አልበሙን አሣትሞ የሚያከፋፍለው ኤሌክትራ ሙዚቃ ቤት ነው፡፡ ባለቤቱ እንደነገሩኝ የመጀመሪያው ሕትመት ወዲያውኑ በመጠናቀቁ ሁለተኛውን አሣትመው ከስር ከስር እያከፋፈሉ ነው፡፡
የመጀመሪያው እትም ምን ያህል ቅጂ ነበር?
25 ሺህ ቅጂ ነው፡፡ ከዛ በኋላ ያለው ግን ከስር ከስር ስለሚሰራጭ ምን ያህል እንደታተመ የተጣራ መረጃ የለኝም፡፡
አልበምህ በወጣ በሦስተኛው ቀን በአዟሪዎች እጅ አልነበረም፡፡ እጥረት መፈጠሩ ጉዳት የለውም?
እጥረቱ የተከሰተው ለአንድ ቀን ቢሆንም ጉዳት ይኖረዋል፡፡ ይህን ያህል ጊዜ አልበሜን ለመስማት የጓጓው አድማጭ ሊገዛ ፈልጎ ገበያ ላይ በማጣቱ የመጀመሪያው ተጎጂ እኔ ነኝ፡፡ አሣታሚው የመጀመሪያውን ሕትመት ቁጥር ሲወስን በሦስት ቀን ውስጥ ያልቃል ብሎ አልገመተም፡፡ የሆኖ ሆኖ አሁን ችግሩ የተስተካከለ ይመስለኛል፡፡ የታተመው ከስር ከስር እየተሰራጨ ነው፡፡ እኔም ገበያው እንዲህ በመሆኑ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡
ማስተሩን ለኤሌክትራ ለመሸጥ ተዋውለህ የቅድሚያ ክፍያ የተቀበልከው ከስድስት ዓመት በፊት መሆኑን ሰምቻለሁ…
የመጀመሪያ አልበሜ አሣታሚና አከፋፋይ ዜድ ሙዚቃ ቤት ነው፡፡ አልበሙ በጣም በመወደዱ ውጭ አገር ኮንሰርት እንዳቀርብ ብዙ ግብዣዎች እየመጡልኝ ነበረኝ፡፡ አልበሜ በወጣ በዓመቱ ከረጅም የኮንሰርት ጉዞ ስመለስ ደግሞ የኤሌክትራ ሙዚቃ ቤት ባለቤት አቶ ተሾመ ጸጋዬ ጠርቶኝ፣ ያለምንም የጊዜ ገደብ ሁለተኛ አልበሜን ሠርቼ ማስተሩን እንድሰጠው የቅድምያ ክፍል ከፈለኝ። አልበሙ ቢዘገይም የወጣው ግን በዚህ ውል መሠረት ነው፡፡
ከሰባት ዓመት በፊት የተዋዋልክበት ክፍያ ከአሁኑ ጊዜ አንፃር አነስተኛ በመሆኑ ውልህን አፍርሰህ ሌላ ውል እንድትገባ ጥያቄዎች ቀርበውልህ እንደነበርና አንተም ፈቃደኛ እንዳልነበርክ መረጃ ደርሶኛል፡፡ ከቀድሞ ውልህ ከፍ ያለ ክፍያ አግኝተህ ነበር?
እንዳልሽው ውሉን ከፈጸምኩ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ እንደሚታሰበው የሚያረካ ባይሆንም የሙዚቃ ኢንዱስትሪው አካባቢ ትንንሽ ለውጦች አሉ፡፡ በተጨማሪም በዛን ግዜ የነበረው የገንዘብ መጠን ከአሁኑ ጋር ሲነጻጸር ዝቅ ያለ ነው፡፡ በዚህ ምክንያት የተሻለ የሚባሉ ክፍያዎችን የያዙ ጥያቄዎች ቀርበውልኝ ነበር፡፡ ነገር ግን ቃል ከገንዘብ የላቀ ዋጋ ስላለው ውል ለማፍረስ አልፈለግሁም፡፡ ቢጂአይ ኢትዮጵያ ደግሞ የማስታወቂያ ሥራውን ለማከናወን የሚያስፈልገውን ወጪ በሙሉ ስፖንሰር በማድረግ ደግፎኛል፡፡ ለዚህም በጣም ላመሰግነው እፈልጋለሁ፡፡
ሁለተኛውን አልበም ለማውጣት ብዙ የዘገየህ ትመስላለህ …
በትክክል ሥራ የጀመርኩት የመጀመሪያውን አልበም ካወጣሁ ከሁለት ዓመት በኋላ ነው- የዛሬ ስድስት ዓመት ገደማ፡፡ የመዘግየቴ ምክንያት ደግሞ ሁሌም አዲስ ነገር ለማውጣት ከመጓጓትና በምሠራው ሥራ ካለመርካት የመነጨ ነው፡፡ የተለያየ ዜማና ግጥም እመርጥና ወድጄው ሠርቼ አስቀምጠዋለሁ፡፡ ሌላ ሠርቼ ደግሞ የቀደመውን መልሼ ሳዳምጠው አላስደስት ይለኛል፤ እንደገና ፈርሶ ሌላ ይሠራል፡፡ እኔ ጥቂት ድርሻ ቢኖረኝም ይህ ሁሉ የሚሆነው ከተለያዩ ዜማ እና ግጥም ደራሲዎች ጋር ነበር፡፡ ይልማ ገ/አብ፣ ሞገስ ተካ፣ቴዲ አፍሮ፣ ጌትሽ ማሞ፣ አለማየሁ ደመቀ፣ ብስራት ጋረደው፣ መሰለ ጌታሁን፣ ታደሰ ገለታ፣ አማኑኤል ይልማና ጌቱ ኦማሂሬ --- በአጠቃላይ አሥር የግጥማና የዜማ ደራሲያን በአልበሙ ላይ ተሳትፈዋል። የጠቀስኳቸው በአልበሙ ላይ አሻራቸውን ያሳረፉትን ነው፡፡ ሠርተውልኝ ያላካተትኳቸው ደግሞ በርካታ ናቸው፡፡ ሃያ አምስት ዘፈን ሠርቼ ነው አሥራ አምስቱን የመረጥኩት፡፡
አልበሙን ሠርቼ ካጠናቀቅሁ በኋላም በቅጂ መብት መከበር ዙርያ ችግር ነበር፣ በዚህ ሳቢያም በአሣታሚዎች ላይ የተፈጠረው ስጋት ቀላል የማይባለውን ጊዜ ወስዷል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የዛሬ ስድስት ዓመት ከሁለት ጓደኞቼ ጋር በከፈትነው “ፋራናይት ናይት ክለብ” ሙሉ ለሙሉ የአስተዳደሩን ሥራ የምሠራው እኔ ነኝ፡፡ በዚህ የተነሳም የጊዜ እጥረት ነበረብኝ፡፡ እንግዲህ እነዚህ ሁሉ ለአልበሙ መዘግየት ምክንያቶች ናቸው፡፡ ሌላው መታወቅ ያለበት ሙዚቃ የስሜት ሥራ ነው - የተመቻቸ ጊዜና ቦታ ይፈልጋል፡፡ ምቹ ጊዜ እና ቦታ ማግኘት ደግሞ ራሱን የቻለ ሥራ ነው፡፡ በዚህ በዚህ ነው የዘገየው፡፡
በአልበም ሥራህ ከሙዚቃ ባለሙያዎች ጋር የነበረህ የሥራ ግንኙነት ምን ይመስላል?
ሥራው አድካሚ፣አስደሳችና አስጨናቂም ነበር። ከባለሞያዎቹ ጋር የነበረኝ ግንኙነት የሥራ ብቻ ሳይሆን የጓደኝነትም ጭምር ቢሆንም ይመሩን የነበሩት የሚፈጠሩት ስሜቶች ናቸው፡፡ አልመጣ ሲለን ድካምና መሰላቸት ይኖራል፡፡ ጥሩ ስንሠራ ደግሞ ደስታና ጨዋታው አለ፤ በቃ በጣም ደስ የሚል ጊዜ እናሳልፋለን፡፡ በተሠራው ስራ ሳንግባባ ስንቀር ደግሞ ልዩነቶች ይፈጠራሉ፤ እንጣላለን፤ ለሌላ ጊዜ እንቀጣጠራለን፡፡ ከዚህ ውጪ ደግሞ ለምሳሌ አንድ ሰሞን አበጋዝ በሰጠኝ የጊዜ ሰሌዳ ሥራውን ለመሥራት ጓጉቼ ስመላለስ፣ እኔ እግሬ ስቱዲዮ በረገጠ ቁጥር መብራት ይጠፋ ነበር። ጠብቄ ጠብቄ ወደ ቤቴ ስመለስና ልክ እቤት ስገባ ይመጣል። አንዳንድ ግዜ ደግሞ ተመልሼ ልክ መንገድ ስጀምር መጣ ይባላል፡፡ ይህ በጣም አብሻቂ እና አስጨናቂ ጊዜ ነበር፡፡ እንግዲህ ከእነዚህ ስሜቶች ጋር በመጨረሻ በፍቅር ሠርተን አጠናቀናል፡፡ ሁሉም ባለሞያዎች ጎበዞችና ጥሩ ባህሪ ያላቸው ነበሩ፡፡
የአድማጩ ምላሽ ምን ይመስላል?
እንግዲህ ከወጣ ገና አንድ ሣምንቱ ነው። በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ የበርካታ ሰዎችን አስተያየት ማግኘት ባይቻልም ከዘመድ ጓደኞቼ፣ከአድናቂዎቼ፣ከአድማጮቼና ከፌስቡክ ጓደኞቼ ከተሰጡኝ አስተያየቶች፣ እንደ ዩቱዩብና ድሬ ቱዩብ ባሉ የምስል ማሳያ ዌብሳይቶች ላይ ከተጻፉ አስተያየቶች እንዳነበብኩት ከሆነ፣ እስካሁን ጥሩ አስተያየት እየተሰጠኝ ነው፡፡ በግጥምና ዜማ እንዲሁም በቅንብሩ ‹‹ጥሩ ነው የሰራኸው›› ተብያለሁ። በድምፅም እድገት አሳይተሃል ብለውኛል፡፡ እስከ አሁን ያለው የሚያበረታታ ቢሆንም ትክክለኛውን አስተያየት ለማግኘት አልበሙ በደንብ እስኪሰማ በቂ ጊዜ ሰጥቶ መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡
“የሸዋንዳኝ ድምፅ ውስጥ የቴዲ አፍሮን ድምፅ ማድመጥ ይቻላል” የሚሉ አድማጮች አሉ፤ አንተ ምን ትላለህ?
እኔ እና ቴዲ በሥራ ብቻ ሳይሆን የልብ ጓደኞችም ነን፡፡ ሥራዎችን የምንሰራው ተማክረን ነው፡፡ የቴዲን የግጥምና ዜማ ችሎታ እኔ መናገር ያለብኝ አይመስለኝም፡፡ በተለይ በመጀመሪያው አልበሜ ከጓደኝነትም ባሻገር ዘጠና በመቶ የሚሆነውን የግጥምና ዜማ ሥራ ሠርቶልኛል፡፡ በሁለተኛው አልበሜም ተሳትፎው እንደ መጀመሪያውም ባይሆንም ቆንጆ የሚባሉ ሥራዎችን ሰጥቶኛል፡፡
እኔና ቴዲ ስታይላችን ተቀራራቢ ነው እንጂ እኔም እራሴን ነኝ ቴዲም ራሱን ነው፡፡ እንዳልኩሽ በመጀመሪያው አልበሜ ላይ ቴዲ በርካታ ግጥምና ዜማ ስለሰጠኝ ሥራዎቼ በእርሱ ዓይን የመታየት ዕድላቸው ሰፊ ነበር፡፡ ለዚህ ነው እንደዚህ ዓይነት አስተያየት የሚሰጠው፡፡ በአዲሱ አልበሜ ከተለያዩ ደራሲዎች ዜማና ግጥም በመውሰድ ስሎው፣ ቺክቺካ፣ ሮክ፣ ሬጌ---የተካተቱበት አዳዲስ ስታይሎችን ሞክሬያለሁ፡፡ ወደ አማርኛ ሥራም የበለጠ ተጠግቻለሁ፡፡
አድማጭ ብትሆን ከአዲሱ አልበም ደጋግመህ ማድመጥ የምትመርጠው የትኛውን ዘፈን ነው?
ሁሉንም (ሳቅ) ለምሳሌ በጣም በተጣበበ ጊዜ ውስጥ ሁለት ዘፈኖች ብቻ ይከፈትልህ ከተባልኩ--- ከስራዎቼ ውስጥ ‹‹ስጦታሽ›› እና ‹‹ስለኔ››ን ልመርጥ እችላለሁ፡፡
ለአልበምህ ማስተዋወቂያ ከተማ ውስጥ የተሰቀለውን ቢልቦርድ ሰዎች ሲያደንቁት ሰምቻለሁ…
ባይገርምሽ ከብዙ የፎቶግራፍ ድካም በኋላ በአጋጣሚ የተገኘ ፎቶ ነው፡፡ ፎቶውን ያነሳኝ አንቶኒዮ ፊዮሬቴ ነው፡፡ ዲዛይኑ ‹‹ላይቭ ዲዛይን›› የሚባል ነው፡፡ ተሰቅሎ ሳየው ለእኔም ደስ ብሎኛል።
ለሙዚቃህ የቪዲዮ ክሊፖች አልሠራህም..
‹‹ስጦታሽ›› ለሚለው ዘፈን የቪዲዮ ክሊፕ ተሠርቶ ተጠናቋል፡፡ የሁለት ወይም የሦስት ዘፈኖች ቪዲዮ ክሊፖች ደግሞ በቅርቡ ተሰርቶ ይለቀቃል፡፡
ከአልበም ሥራዎች ውጭ ኮንሰርቶች የት አቅርበሃል..
የውጭ ጉዞ የጀመርኩት የመጀመሪያውን አልበም ከማውጣቴ ቀደም ብሎ ነው፡፡ ሙዚቃ ስጀምር የእንግሊዘኛ ዘፈን እና ጥቂት አማርኛ እጫወት ስለነበር ከአገር ውስጥ የመድረክ ሥራዎች በተጨማሪ ጣልያን፣ ጅቡቲ፣ ኬንያ እና ዱባይ ተጉዤ ሠርቻለሁ፡፡ አልበሙ ከወጣ በኋላም በአገር ውስጥ የተለያዩ የመድረክ ሥራዎችን አቅርቤአለሁ። ከኢትዮጵያ ውጪ ደግሞ ግብጽ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ባህሬን፣ ዱባይ፣ አቡዳቢ፣ እስራኤል፣ ስዊድን፣ እንግሊዝ፣ ኖርዌይ፣ ሆላንድ እንዲሁም በአሜሪካ ከአሥራ ሁለት ግዛቶች በላይ እና በሌሎች አገሮች በተደጋጋሚ ለኮንሰርት እየተጋበዝኩ ሠርቻለሁ፡፡ “ፋራናይት”ን ከከፈትኩ በኋላም በየሣምንቱ ሐሙስ እየተጫወትኩ ነው፡፡
ናይት ክለብ የምትጫወተው የራስህን ሥራዎች ብቻ ነው?
አይደለም፡፡ ከራሴ አልበም ውጪ በዋናነት የአርቲስት መሐሙድ አህመድን፣ የአርቲስት ንዋይ ደበበን፣ የአርቲስት ጌታቸው ካሣና ሌሎች ዘፋኞችን ሥራዎችም እጫወታለሁ፡፡
የዩኒቨርስቲ ትምሕርትህን አቋርጠህ ነው ወደ ሙዚቃ የገባኸው፡፡ ቤተሰብ አልተቃወመም?
ስሜቴ ወደ ሙዚቃ የተሳበው አስረኛ ክፍል ስደርስ ነበር፡፡ ያን ግዜ አሁን በሕይወት የሌለው አባቴ ከፍቶት ነበር፡፡ ዩኒቨርስቲ ስገባ ግን ዶርም ውስጥ አድር ስለነበር ነገሮች ምቹ ሆኑልኝ፡፡ እየተደበቅሁ በመውጣት ሙዚቃውን ገፋሁበት። እንዲህ እንደማደርግ አባቴ ባወቀ ጊዜም ደስተኛ አልነበረም፤ ሊደግፈኝም ፈቃደኛ አልሆነም። በመጨረሻ ቆርጬ ወደ ሙዚቃው መግባቴን ሲያውቅ ግን ምንም ሊለኝ አልቻለም፡፡
አዲሱ አልበም ከወጣ በኋላ የውጭ ኮንሰርቶች ግብዣ አልመጣልህም?
ውጭ አገር ከሚገኙ ፕሮሞተሮች ጋር ትውውቁም ጓደኝነቱም ስላለን ገና አልበሙን እንዳገኙ ነው መደወል የጀመሩት፡፡ በእኔ በኩል ግን ኮንሠርት ለመሥራት አልበሙ በደንብ መሰማቱን እና መወደዱን ማረጋገጥ አለብኝ፡፡
አሁን ደግሞ የሙስሊም ፆም ገብቷል (በዚህ አጋጣሚ ለእስልምና እምነት ተከታዮችና ለጓደኞቼ መልካም የፆም ጊዜ እመኛለሁ) ፆሙ ሲወጣ የአዲሱ አልበም ምርቃት ይኖረኛል፡፡ ኮንሠርት የመሥራት ዕቅዴም ከዚያ በኋላ የሚወሰን ይሆናል፡፡
ቤተሰብ አልመሰረትክም፤ ትዳርን ፈራኸው እንዴ?
ኧረ አልፈራሁም! አሁን የምር እያሰብኩበት ነው፡፡ በቅርብ አዲስ ነገር ይኖራል የሚል ተስፋ አለኝ፡፡

Published in ጥበብ

ለአገራቸው ነፃነት ከጣልያን ጋር የተዋጉ አርበኛ ታሪክ
ሁለት ልጆቻቸው በቀይ ሽብር ተገደሉ፡፡
ልጆቼን ልቅበር ሲሉ እስር ቤት ተወረወሩ፡፡
ሚስታቸው በሃዘን ብዛት ህይወታቸው አለፈ፡፡
አንድ የቀረቻቸው ልጅ የት እንደገባች አያውቁም፡፡
ስድስት ዓመት ታስረው ሲወጡ ቤታቸው ፈርሷል!

አቶ መኮንን ብሩ ይባላሉ - የ99 ዓመት አዛውንት ናቸው፡፡ በወሎ ክፍለሀገር አማራ ሳይንት ውስጥ የተወለዱት አቶ መኮንን፣ አምስት መንግስት አይቻለሁ ይላሉ፡፡ በ1928 ዓ.ም ፋሽስት ጣሊያን ኢትዮጵያን ሲወር የ20 ዓመት አፍላ ወጣት እንደነበሩ የሚያስታውሱት አዛውንቱ፤ በደርግ ዘመ ሁለት ወንድ ልጆቻቸው በቀይሽብር እንደተገደሉባቸው ይናገራሉ፡፡ ይሄም ሳያንስ ግን “ሬሳቸውን ወስጄ ልቅበር” በማለታቸው በማዕከላዊ እስር ቤት ለስድስት ዓመት ታስረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የሚኖሩት “የወደቁትን እናንሳ” በተባለ አዛውንትን ሰብሳቢ ማህበር ውስጥ ሲሆን የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ስለ ጣሊያን አርበኝነታቸው፣ ስለኖሩባቸው አምስት መንግስታትና ስለህይወታቸው ቃለምልልስ አድርጋላቸዋለች፡፡ ከ15 ዓመት በፊት የተመሰረተው “የወደቁትን እናንሳ” የተሰኘ ማህበር በበጐ ፈቃደኞች የሚደገፍ ሲሆን በአሁን ሰዓት 46 ሴትና እና 34 ወንድ አረጋዊያንን በመጠለያ፣ በምግብ፣ በህክምናና በእንክብካቤ እየደገፋቸው ይገኛል፡፡ በማህበሩ ከሚረዱት አዛውንቶች መካከል ከ25 ዓመት በላይ በመምህርነት ያገለገሉ፣ የፖሊስ ኦርኬስትራ የሙዚቃ አባል የነበሩ፣ በአርበኝነት ዘምተው የጣልያንን ወራሪ ኀይል የተፋለሙና በህግ ባለሙያነት ያገለገሉ ይገኙበታል፡፡ ለዛሬ ከ99 ዓመቱ አርበኛ አቶ መኮንን ብሩ ጋር ያደረግነውን ጨዋታ እነሆ፡፡

 በጣሊያን ወረራ ወቅት አርበኛ እንደነበሩ ሰምቻለሁ ---

እንዴታ! አምስት አመት ሙሉ ተዋግቻለሁ፡፡
እንዴት ነው የዘመቱት?
አባቴ ቀኝአማች ብሩ ሀይለኛ አርበኛ ነበሩ፡፡ በጦርነቱ ጣሊያኖች አባቴን ሲገድሉብኝ እጅግ ተቆጣሁ፣ ደሜ ፈላ፡፡ በወቅቱ የ20 ዓመት ወጣት ነበርኩ፡፡ ማቄን ጨርቄን የምለው አልነበረኝም፡፡ ጫካ ገባሁና መዋጋት ጀመርኩኝ፡፡
ከየት አካባቢ ነው ወደ ጦርነቱ የሄዱት?
የተወለድኩት ወሎ ውስጥ አማራ ሳይንት ነው፡፡ ጦርነቱን የተቀላቀልኩትም ከዚያ ሄጄ ነው፡፡
በላይ ዘለቀን ያውቁታል ይባላል፡፡ እውነት ነው?
አሳምሬ አውቀዋለሁ እንጂ እንዴት አላውቀውም!
አብራችሁ ዘምታችኋል እንዴ?
አብረን አልዘመትንም፡፡ እኔ እራያ አዘቦ፣ መሆኒ፣ ሸዋ፣ መንዝ፣ መራ ቤቴ፣ አህያ ፈጅ ዶባ እየተዘዋወርኩ ራያው ከፈለ ከተባለ የጦር መሪ ጋር ነው የተዋጋሁት፡፡ ጐበዝ የጦር መሪ ነበር፡፡ በላይ ዘለቀ ግን አባይ በረሃ ላይ ነበር፡፡ ግን ተገናኝተን እናውቃለን፡፡ በደንብ ነው የማውቀው!
ድል ካደረጋችሁ በኋላ ስለነበረው ሁኔታ ያጫውቱኝ-----
ጃንሆይ “አገርህን ለመጠበቅ በጫካ ያለህ ወደ እኔ ተሰብሰብ” ብለው ሲጣሩ፣ ከነበርኩበት ተነስቼ ከጓደኞቼ ጋር መጣሁ፡፡ እርሳቸው ውጭ አገር ከርመው መምጣታቸው ነበር፡፡ እናም አርበኛው ሁሉ በጠቅላላ አዲስ አበባ ገባና ተሰበሰበ፡፡ ጃንሆይ ጃን ሜዳ መጡ፣ በሬው ሁሉ ታረደ፣ ተደገሰ፡፡ ድግሱ ሲያልቅ እዚሁ ለትንሽ ጊዜ ቆዩ ተባልን፡፡ ግን ማንም የሰማቸው የለም፣ ሁሉም በየሀገሩ ሲበታተን እኔም አማራ ሳይንት ገባሁ፡፡
በወቅቱ ጡረታ ምናምን አልነበረም ? ከድል ስትመለሱ ማለቴ ነው---
ደሞ የዛን ጊዜ ጡረታን ማን ነገሬ ይለዋል! መሬት ሞልቷል፣ ገንዘብ ሞልቷል፣ ከብት እንዳፈር ነው፡፡ አሁን እኮ ነው ሁሉ ነገር ችግር የሆነው፡፡ እናም ዝም ብለን አገራችን ገባን፡፡
ታዲያ እንዴት አዲስ አበባ ተመለሱ?
ከተማ ልኑር ብዬ ነው የመጣሁት፡፡ ከዚያም ሚስት አገባሁ፣ ሁለት ወንድና እና አንድ ሴት ልጆች አፍርቼም በሜካኒክነት ሙያ እየሰራሁ ልጆቼን ማስተማር ጀመርኩኝ፡፡
ከዚያስ?
ከዚያማ --- ሁለቱ ወንዶች ልጆቼ 12ኛ ክፍልን ጨረሱ፣ ደረሱልኝ ስል ተቀጠፉብኝ፡፡
እንዴት?
በቀይሽብር ጊዜ ከጨርቆስ አምጥተው ከጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን አለፍ ብሎ ባለው እራስ እምሩ ቤት አጠገብ በሚገኘው ሜዳ ላይ አምጥተው ገደሏቸው፡፡ እያበድኩኝ ሄጄ የልጆቼን እሬሳ አንስቼ እቀብራለሁ ብል ተከለከልኩኝ፡፡ ከዚያም ሙግት ገጠምኩኝ፡፡ እምቢ ካልክማ አሉና --- ማዕከላዊ የሚባል ፖሊስ ጣቢያ ያለጠያቂ ለስድስት ዓመት ታሰርኩ፡፡
ባለቤትዎና ሴት ልጅዎስ?
ባለቤቴ በልጆቿ ሞት ሀዘን ገብቷት እህህ… ህ ስትል፣ እኔ እስር ቤት እያለሁ ሞተች፡፡ እናቷንና ወንድሞቿን በሞት፣ አባቷን በእስራት የተነጠቀችው ሴት ልጄ የት እንደገባች፣ ምን እንደበላት አላውቅም፡፡ በህይወት ትኑር ትሙት የማውቀው ነገር የለም፡፡ እስከዛሬም የእግር እሳቴ ናት፡፡ ስድስት አመት ታስሬ ስወጣ እንኖርበት የነበረው ቤት በመንገድ ስራ ምክንያት ፈርሶ አገኘሁት፡፡ መውደቂያ አጣሁ፣ ችግርና ቁስቁልናው ተስፋ አስቆርጦኝ ሜዳ ላይ ወደቅሁኝ፡፡ ለረጅም ጊዜ ሜዳ ላይ ዝናብና ፀሐይ ሲፈራረቅብኝ ነው የኖርኩት፡፡
አሁንስ? ወደ እዚህ ማህበር ከመጡ በኋላ ኑሮ እንዴት ነው ?
እዚህማ አለም ነው፡፡ እበላለሁ አጠጣለሁ፣ እታጠባለሁ፡፡ ሁሉም ነገር ጥሩ ነው፡፡ በደንብ ይንከባከቡኛል፡፡
አሁን እርግጠኛ 99 ዓመት ሞልቶዎታል?
እንዴ ምን ትላለች! ጣሊያን ሲወረን 20 አመቴ ነው እያልኩሽ! አምስት መንግስት አይቻለሁ እኮ ነው የምልሽ፡፡
አምስት መንግስት ሲሉ--- ከምኒልክ ጀምሮ ነው?
ከዘውዲቱ ጀምሬ አለሁ፡፡ ንግስት ዘውዲቱን አውቃታለሁ፡፡ የስፌት ባርኔጣ ነበር የምታደርገው፡፡ በጣም አደገኛ ሴት ነበረች፡፡
አደገኛ ናት ሲሉ ምን ማለትዎ ነው?
አይ የዛሬ ልጆች! በቃ አደገኛ ናት አልኩሽ አደገኛ ናት፡፡
አምስት አመት ሲዋጉ በጥይት ተመተው ያውቃሉ?
አንድም ቀን አልተመታሁም፡፡ ጥይቱ በግራ በቀኝ ሲያፏጭብኝ አንድም ቀን ተመትቼ አላውቅም፡፡
ኃይለኛ ውጊያ ውስጥ አልነበሩም ማለት ነው? እንዴት ሳይመቱ ቀሩ?
እኔ ምን አውቃለሁ፡፡ እየነገርኩሽ --- በደረቴ ላይ እየሄደ አይመታኝም ነበር፣ ይስተኛል፡፡ ምክንያቱን ግን አላውቀውም፡፡
እርስዎስ ይስታሉ ወይስ አልሞ ተኳሽ ነበሩ ?
ኧረረረ…ስለኔ አልሞ ተኳሽነት ጓደኞቼ በነገሩሽ እንዴት ጥሩ ነበር! (ከንፈራቸውን በተረፉት ጥርሶቻቸው እየነከሱ) ስሜ መኮንን ብሩ ነው ብዬሻለሁ፡፡ በኋላ ጓደኞቼ ቃኘው መኮንን የሚል ስም አወጡልኝ፡፡ ለምን አወጡልህ ብትይኝ --- ጦርነት ከመጣ ወደ ፊት መሄድ እንጂ ድል አርገናል ብዬ ወደ ኋላ አልመለስም፡፡ በቃ ወደ ፊት መግፋት ነው፡፡ ጥይቱ እየተንፏፏ እንኳን ቢሆን ዝም ብዬ እሄዳለሁ፡፡
ካዩዋቸው መንግስታት ጥሩ ነው፣ አስደስቶኛል የሚሉት የትኛው ነው?
እሱን አትጠይቂኝ! (በኃይለቃል) ይህን ቢያወሩት ምን ይሠራል! በቃ ወደ ሌላ ጨዋታ --- ወሬ ታለሽ!
አብዛኛዎቹ እርስዎ ያሉበት ክፍል ውስጥ ያሉት አረጋዊያን ራሳቸውን ችለው አይንቀሳቀሱም ፡፡ እርስዎ ግን ብቻዎን ይንቀሳቀሳሉ ---
እንዲህ ናትና--- በደንብ ነዋ! (ከተቀመጡበት አልጋ ላይ ተስፈንጥረው ወረዱ) አታይም እንዴ! ገና ጐረምሳ እኮ ነኝ! እንዴት ትቀልዳለች ይቺ ልጅ!
ድሮ በጣሊያን ወረራ ጊዜ ስትዋጉ ፉከራ፣ ሽለላና ቀረርቶ በሽበሽ ነበር፡፡ አሁን ካስታወሱት እስኪ ትንሽ ይፎክሩልኝ ----
ምን እባክሽ ---- ፉከራና ቀረርቶ ሞልቷል፡፡ ግን አሁን ምን ያደርግልኛል? ጉሮሮዬ ገጥሟል-- ሰውንም መረበሽ ነው--- ይቅር
ለእርጅና እጅ አልሰጥም--- ጐረምሳ ነኝ አላሉም እንዴ?
ታዲያ ያልኩ እንደሆነሳ! በቃ ፉከራና ሽለላ አሁን ይቅር ነው ያልኩት---የተኙትን ሰዎች እረብሻለሁ፡፡ ጉሮሮዬም ትንሽ ችግር አለው፡፡
ከዚህ በኋላ ስንት ዓመት መኖር ይፈልጋሉ?
አሁን ሞት መጥቶ ቢወስደኝ ደስታውን አልችለውም፡፡
ለምን?
ተይ የኔ ልጅ--- ከዚህ በላይ መኖር አይረባም፡፡ ምንም እንኳን አሁን የጎደለብኝ ነገር ባይኖርም እሰው እጅ ላይ ወድቆ አንሱኝ ጣሉኝ ማለት ትንሽ ደስ አይልም፡፡ እንዲሁ ቅልጥፍ እንዳልኩ ብሄድ ደስ ይለኛል፡፡
ግን ለምን ተስፋ ቆረጡ?
በቃ ቆርጫለሁ፡፡ ሞት ግን እኔን አልፈልግም አለ፡፡ መሬት ላይ ወድቄ እንዲህ እንደማያቸው ሰዎች (እርሳቸው ክፍል ውስጥ ያሉትን ተረጂዎች ማለታቸው ነው) ሳልሆን ብሞት ብዬ ፈጣሪን ብለምነው እምቢ አለ፡፡ ከዚህ በላይ ምን እንደምሠራለት አላውቅም፡፡ በቃ ሰው ራሱን እንደቻለ ነው መሞት ያለበት፡፡

 

Saturday, 13 July 2013 11:45

የካርታ ጨዋታ

ሼልፍ አለችኝ፡፡ “አለኝ” ብዬ የምተማመንባት አይደለችም፡፡ እንደ አቅሚቲ የተወሰኑ መጽሐፍት ሰባስቤ ሰካክቼባታለሁ፡፡ ከኑሮ እና ከሌላ አልባሌ ግራ መጋባት የተረፈኝ ገንዘብ ሲኖር አይኔን የሳበውን የመጽሐፍ ሽፋን ተመርኩዤ እገዛና እጨምርባታለሁ፡፡ እንደ ሁላችሁም፤ እኔም የሽፋን አምልኮ ተከታይ ነኝ፡፡ የሰበሰብኳቸው መጽሐፍ ከሁለት የቋንቋ አቅጣጫ የመጡብኝ/ልኝ ናቸው፡፡ አንዱ ያው እንግሊዝኛ መሆኑ ነው፡፡ የተቀሩት፤ አሁን እየፃፍኩ ባለሁበት ቋንቋ የታተሙ ናቸው፡፡ መጽሐፍቱ የተደረደሩት የህትመት ዘመንን ቅደም ተከትለው አይደለም፡፡ እንደዘውጋቸው ወይንም እንደይዘታቸውም አይደለም፡፡

ቅርፃቸውም… ለአደራደራቸው ስምምነት ምክንያት አይሆንም፡፡ ተመለከትኳቸው፡፡ ከመመሳሰል ይልቅ መራራቃቸው አየለብኝ፡፡ ሼልፉ ላይ በተገኘው ክፍተት የተሻጡ፤ ከተገኘው አዟሪ የተሸጡልኝ ናቸው፡፡ አለመመሳሰላቸው፣ በተደረደሩበት… እንደአጋጣሚ የያዙት ተቃርኖ መሰጠኝ፡፡ ልጽፋቸው ተነሳሁ፡፡ አይኔ በመጀመሪያ ያረፈበት መጽሐፍ የእኔ የትኩረት ምርጫ ነው፡፡ መፅሐፉማ ምርጫ የሌለው ግዑዝ ነው፡፡ “ኦሮማይ” ይላል፡፡ “ኦሮማይ” ከሚለው አርዕስት ጋር የሚተሳሰሩ ለዘመናት፣ የተከማቹ መረጃዎች ትዝ አሉኝ፡፡ በዓሉ ግርማ…ሀዲስ፣ ከአድማስ ባሻገር…በደብረ ዘይት መንገድ ላይ ቆማ የተገኘችው ቮልስ ዋገን…የተሰወረው እና የደረሰበት ያልታወቀው ደራሲ… ሁሉም ትዝ አለኝ፡፡ ከኦሮማይ ጐን የተሰካው መጽሐፍ ግን መሆን ያልነበረበት ነው፡፡ “ዘ ማይንድ” የሚል በዶ/ር አቡሽ የተፃፈ ራስን ለማነቃቃት (motivation) ይጠቅማል ተብሎ የተፃፈ… “የአንቃ-አሩጥ” መጽሐፍ ነው፡፡

ራስን ለማነቃቃት ተብሎ የተፃፈ መጽሐፍ ከ”ኦሮማይ” ጋር መዳበሉ ለበአሉ ግርማ ምን ይፈይድለታል? ብዬ በጠማምኛ አሰብኩ፡፡ የበአሉ መነቃቃት፤ ወይንም ከሞት ተመልሶ መምጣት… ለማን ብልጽግና ይፈጥራል? ብዬ በዳኛቸው ወርቁ’ኛ “ፈደስኩ”፡፡ አዲስ መጽሐፍ ጠረጴዛ ላይ ሼልፉ መሃል ቦታ አጥቶ ሲጠብቅ አየሁ፡፡ በይስማይከ ወርቁ የተፃፈ ከማተሚያ ምጣድ ወደ አንባቢ አይን በቅርቡ ማእድ የተቀላቀለ፣ ያጨናነቀ መጽሐፍ፡፡ “ክቡር ድንጋይ” ይላል አርእስቱ፡፡ “በአሉ ከተሰወረበት ተመልሶ የመጣው ይስማዕከን ሆኖ ነው” የሚል ጭምጭምታ የሰማው ጆሮዬ… በአፌ በኩል ወደ ፈገግታ ሲለወጥ ተሰማኝ፡፡ መጽሐፉን አንስቼ ከዶ/ር አቡሽ መፅሐፍ አስከትዬ አስቀመጥኩት፡፡ “ኦሮማይ” ራሱን የብልጽግና ጥበብ ካስተማረ በኋላ “ክቡር ድንጋይ” ሆኖ መሸጡን አመልካች ይሆን ድርጊቴ?...ሊሆን ይችላል፡፡ በተርታው ወደ ግራ በመቀጠል የተሰተረው መጽሐፍ ላይ ላተኩርበት በማነጣጠር ላይ ሳለሁ መጽሐፉ ቅርፊት (ሽፋን) የሌለው ሆነብኝ፡፡ አውጥቼ ከምመለከተው… የትኛውን መጽሐፍ ሊሆን እንደሚችል በአቦ ሰጡኝ ብገምት ለጨዋታዬ ብዙ አማራጭ እንደሚከፍት ገመትኩኝ፡፡

ሽፋን አልባውን መጽሐፍ እንደ “ጆከር” ቆጠርኩት፡፡ እንደ ፍልስፍና መጽሐፍ የጆከርን ባህሪ በደንብ አድርጐ የሚላበስ የለም፡፡ መጽሐፉ በገጽ ብዛትም በቁመትም አጭር ነው፡፡ የፍልስፍና መጽሐፍ ከሆነ/ ቢሆን የምዕራባዊያን ፍልስፍና ሳይሆን ኢትዮጵያዊ ፍልስፍና መሆኑ አያጠራጠርም፡፡ የኢትዮጵያዊ ፍልስፍና በዘረ-ያዕቆብ ተጀምሮ እዛው ዘረ-ያዕቆብ ላይ ይጠናቀቃል፡፡ በአጭሩ… በጥቂት ገፆች፡፡ ጆከሩን መዝዤ ውስጥ ገፁን ስመለከተው የአቤ ጉበኛው ታዋቂ መጽሐፍ “አልወለድም” ሆነና አረፍኩት፡፡ የገዛሁት ከአሮጌ ተራ ነው፡፡ ተራው ራሱ አሮጌ አድርጐታል፡፡ “አልወለድም” ከሚለው ተጨባጭ አርዕስት ጋር ስፋጠጥ፤ ቅድም በምናቤ የሳልኩትን የፍልስፍና መጽሐፍ ቢሆንልኝ የሚለውን ምኞቴን መርሳት ቢኖርብኝም፣ መርሳት ግን አልቻልኩም፡፡ ተጨባጩ እና የማይጨበጠው ተደባልቀው ሌላ ትርጉም በውስጤ መሳል ወይ ማሳል ጀመሩ፡፡ ፍልስፍናና ዘረ - ያዕቆብ በኢትዮጵያ “አልወለድም” አሉ፤ የሚል ትርጉም፡፡ ትርጉሙን ወዲያው ረሳሁት፡፡

ጨዋታው ቁማር ነው፡፡ በሳንቲም ወይንም በካርታ ወይንም በDice የሚደረግ ቁማር ሳይሆን… በመጽሐፍ ነው፡፡ መጽሐፍቶቹ እንደ ካርታ ተደርድረዋል፡፡ ውልግድግድ ያሉ ጥርሶች ቢመስሉም፤ እኔ እንደ አሻኝ አስተካክዬ በጽሑፍ መልክ እወርዳቸዋለሁ፡፡ ቁማሩ የሃሳብ ነው፡፡ ተጫዋቹ እና የጨዋታው ህግ ከእኔ… መጫወቻው ግን ከመጽሐፍት መደርደሪያው… የመጡ ናቸው፡፡ ጨዋታው ይቀጥላል፡፡ ከ”አልወለድም” ጐን የሰለሞን ዴሬሳ “ዘበት እለፊቱ” አለ፡፡ ዘመናዊ ጥበብ እንዲወለድ አስተዋጽኦ በማድረጉ ከአቤ ጉበኛው ጋር መቀመጡ ተገቢ መሰለኝ፡፡ አልወለድም ያለውን እንቢተኝነት “በልጅነት” ያዋለደው ዶክተር እሱ ስለሆነ፡፡ በአንድ ተርታ መቀመጥ ይችላሉ፡፡ አንዱ “ኤ” ጦር ሌላው “ኬ” ጦር ቢሆኑም፤ ንጉሱ እና ጦር መሳሪያው ከተገናኙ ጦርነት መፍጠሩ አይቀርም፡፡

በአልወለድም እና ትወለዳለህ መሐል የጥበብ ጦርነት ተከስቶ ነበር ይላሉ፤ የስነፅሁፍ ታሪክ ዘካሪዎች፡፡ ከሁለቱ ተቃራኒ ሃሳቦችን አንድ ለመምረጥ ሶስተኛ ሀሳብ ያስፈልጋል፡፡ ሶስተኛው የለም፡፡ ከሁለቱ መፅሐፍት በመቀጠል በሼልፌ ላይ ተደርድሮ ያገኘሁት የደስቲዮቪስኪ “crime and punishment” የተባለው ገናና ድርሰት ነው፡፡ በ”አልወለድም” መፅሐፍ እና በ”ልጅነት” መሃል ለተፈጠረው የጥበብ አቋም ግጭት ማን ወንጀለኛ እንደሆነ ማወቅ ካልተቻለ እንዴት “ወንጀለኛውን መቅጣት” ይቻላል?... ዘመነኛ መፅሃፍ “የመኝታ ቤት ሚስጥር” በሚል አርዕስት ስፍራውን ይዞ ተሸጉጧል፡፡ ከዚህ መፅሃፍ ጋር የሚሄድ ነገር መፈለግ እንዳለብኝ አመንኩ፡፡ የመኝታ ቤት ሚስጥር የሚያጋልጠው ምንድነው? ብዬ የመፅሃፍቱን ጠርዝ በዓይኔ እንደ ፒያኖ መምታት ጀመርኩ፡፡ ትክክለኛ ድምፅ በሌላ ረድፍ ላይ መፅሐፍን ተመስሎ አገኘሁ፡፡ የመኝታ ቤትን ሚስጥር የሚያጋልጥ “big brother” ነው፡፡ ቢግ ብራዘር የሚለውን መፅሃፍ ያነሳሁት ከአባቴ ሼልፍ ነበር፡፡ የመኝታ ቤትን ሚስጥር የሚገልፀውም ሆነ የሚያደንቀው ቢግ ብራዘር ነው፡፡ ጎን ለጎን አስደግፍኳቸው፡፡ የናዚ ወንጀለኞችን የከሰሰው የኑረንበርግን ፍርድ ሂደት የሚያትት “the “Nuremburg Trial” ከሚለው መፅሃፍ ጎን ብደረድረው “ትሪስ” የሚሰራ… የመፅሀፍ ካርታ በዓይኔ ማሰስ ነበረብኝ፡፡ “ኢህአዴግን እከስሳለሁ” የሚል መፅሃፍ ገዝቼ እንደነበር ትዝ አለኝ፡፡ ሁለቱን አንድ ላይ ለማስቀመጥ ግን ደበረኝ፡፡ አይመጣጠኑም፡፡

በክስም በክስ አወቃቀርም፡፡ በገፅም፡፡ የማይረባ ክስ የያዘው መፅሃፍ፣ የረባ የገፅ ብዛት አለው፡፡ እና ተገላቢጦሽ፡፡ የናዚ ወንጀለኞችን የፍርድ ሂደት ከሚዘግበው መፅሃፍ ጎን የገስጥ ተጫኔን “ነበር” መደርደር የተሻለ ሳይሆን አይቀርም፡፡ የተሻለ ካርታ ከወጣልኝ አደራደሬን መለወጥ እችላለሁ፡፡ “ነበር” የሚለውን መፅሃፍ የሚመስሉ ብዙ “ነበረኝነትን” የሚተርኩ መፅሐፍት አየሁ፡፡ ተራራን ያንቀጠቀጠ ትውልድ፣ትግላችን፣ አጥፍቶ መጥፋት፣ የደራሲው ማስታወሻ…፣… የተደጋገመ ካርታ (ዶፒዮ) ይመስላሉ፡፡ … ብከምራቸው ሰማይ የሚነካ ማማ አክለው (tower in the sky) ሳይቆለሉ አይቀሩም፡፡ “ነበር”ን በየፈርጁ ከመደጋገም… “ሆኗል” የሚል አዲስ ካርታ በመፅሃፍ መልክ ብስብ ምናለበት ብዬ ፀለይኩ፡፡ ፀሎቴ “እንቅልፍ እና እድሜ” የተቀላቀለበት እንዲሆን በእውቀቱ ሥዩምን አስከተልኩት፡፡ አስገባሁት፡፡ በ“ነዋሪ አልባ ጎጆዎች” በኩል፤ አስገባሁት፡፡ በመፅሐፍ ካርታዎቼ መሃል፡፡ አስገባሁት፤ ዳግመኛ “መግባት እና መውጣት” እንዳይችል አድርጌ፡፡መፅሐፍቱ ካርታ ናቸው፡፡ እየታዩ የሚደረደሩ እንጂ የሚነበቡ አይደሉም፡፡

የሚነበቡ ቢሆን እንኳን፤ እርስ በራሳቸው ግን አይናበቡም፡፡ አይስማሙም፡፡ መፅሐፍቱ በይዘት ወይንም በቅርፅ ወይንም በገፅ ብዛት የማይለኩ፣የማይሰካኩ ከሆነ የምንመዝናቸው በኪሎ መሆን አለበት፡፡በኪሎም ቢሆን ያን ያህል ኪሎ የሚያነሳ መፅሃፍ አላየሁም፡፡ ከ16-100 ሉክ ደብተር ናቸው፡፡ እንደ ፈረንጆቹ (hard cover) ቅርፊት ያለው እንኳን ለአመል አይገኝም፡፡ በዋጋ ተመናችሁ መተማመንም ዋጋ የለውም፡፡ በኪሎ ወፍራም የሆነ መፅሐፍ ድሮ በታተመበት ወቅት የተሰጠው ዋጋ አሁን ላይ ሲታይ ቀልድ ይመስላል፡፡ ዝም ብዬ ካርታውን መጫወት ይሻለኛል፡፡ መበወዝ እና መደርደር፡፡ ተደርድሮ አልስማማ ሲል ማሰባጠር፡፡ ሲሰባጠሩ እና በአርዕስቶቻቸው አማካኝነት ሲቀባጥሩ መመልከት፡፡ ያልተናገሩትን… እንዲናገሩ ማድረግ፡፡

በውስጣቸው የያዙት ይዘት ከፍ ያለም… ዝቅ ያለም ዋጋ የለውም፡፡ ለማመዛዘኛነት አይጠቅምም፡፡ በካርታ ጨዋታው፤ ይዘትም ሆነ ቅርፅ ብዙም ሳይኖረው በሆነ ተአምር “ልብ” “ጦር” “ጦሩ” “ዳይመንድ” ሆኖ ሊገኝ ይችላል፡፡ “ልቡ” ካህሊል ጂብራን (ከሆነ) በተበወዘው አደራደር “ልቡ” “የጦርነት ጥበብ” መፍጠሪያ ሆኖ ሊገኝ ይችላል፡፡ ወይንም “የጦርነት ጥበቡ” ክቡር ድንጋይ ሊሆን ይችላል፡፡ ክቡር ድንጋይ፤ ድንጋይም ሆኖ የሚከበረው በገበያ ላይ ዋጋ ስላለው ነው፡፡ እየበወዝኩ የደረደርኳቸው የመፅሐፍት ካርታዎቼ እርስ በራስ ባይስማሙም… ለቅጽበት ግን ከትርጉም አልባ የተናጠል ማንነታቸው ያለፈ የእጣ ፈንታ፣ የአጋጣሚ ትስስር እና ዝምድና የፈጠሩ ይመስላሉ፡፡ ስራ መፍታት ለፈለገ የእኔ አይነት የማጣረዝ ፍቅር ላዛለው ሰው ምናቡን በማዝናናት ሰበብ የካርታ ጨዋቶቹ ስራ ያሸክማሉ፡፡ ሰፊ ያልሆነ ስራ፡፡

Published in ጥበብ
Page 8 of 13