Saturday, 27 July 2013 13:57

‘አባባ ገፋ፣ ገፋ…’

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ስሙኝማ…መቼም ጉዳችን አያልቅ! ብሎ፣ ብሎ የኬት መውለድና አለመውለድ ‘ጉዳያችን’ ሆኖ ይረፍ! እንደው አሰሳቸውንም፣ ገሰሳቸውንም ስንሰበስብ እያዩ… “እናንተ ብሎ ባለድሪምላይነር…” ቢሉን ምን ይገርማል! ለሶፍትዌር ባለሙያዎቻችን ሀሳብ አለን…ከመከረኛው ኢንተርኔት ላይ ለእኛ የሚሆነውና የማይሆነውን እየለየ ‘ፊልተር’ የሚያደርግ ሶፍትዌር ይሥሩልንማ!
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ይሄኔ እኮ ጎረቤታችን ስትሰቃይ ከርማ የወለደችን ሴት አይደለም “እንኳን ማርያም ማረችሽ!” ልንላት…አለ አይደል… “አንድ ለራስ እንኳን በቀን ሁለቴ መመገብ አስቸጋሪ በሆነበት ጊዜ የምትወልደው… ሙጃ ልታበላው ነው!” ምናምን የምንል እንኖራለን። እናላችሁ… “ገንፎ ብሉ…” ባልተባልንበት… “እልል በሉ፣ ኬት ወንድ ልጅ ከእነቃጭሉ ዱብ አደረገች…” አይነት ነገር አሪፍ አይደለም፡፡
ስሙኝማ…የድሪምላይነሩን ነገር ተከትሎ ኢንተርኔት ላይ እየተሰጡ ያሉ አስተያያቶች…አለ አይደል…ዓለም አሁንም እንዴት ‘እንደሚተረጉመን’ አሪፍ ማሳያዎች ናቸው፡፡ “አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች…” የሚሉት አዲስ አበባ ብቻ እንደሚቀር ልብ ይባልማ! በየስፖርቱም፣ በየምናምኑም “ዓለም በጉጉት የሚጠብቀው…” ምናምን የምንለው ሁሉ ‘ሳይንስ ፊክሺን’ እንደሆነ ልብ ይባልልንማ! ቂ…ቂ…ቂ… (በተለይ…ግርም የምትለኝ ነገር ምን መሰላችሁ…የሆነ እኛን የሚመለከት ነገር በሆነ የኤፍ.ኤም. ፕሮግራም ላይ ይጠቀስና ምን ይከተላል መሰላችሁ…“ዓለምን እያነጋገረ ያለ ጉዳይ…” ይባላል። ዓለምማ አይደለም ‘ራዲዮናችን’… የኢትዮዽያ ድሪምላይነር አውሮፕላን… ምናምን ሲባል ምን ይል መሰላችሁ… አንዱ ‘ፈረንጅ’ በመከረኛው ፌስቡክ ላይ እንደለጠፈው… “Dreamliner! Ethiopia! You must be kidding me!” ይላል፡፡ የእኛ ነገር እንዲሁ ነው፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ዘንድሮ የ‘መሳም’ና የ‘ማቀፍ’ ትርጉሞች እየተለዩላችሁ ነው፡፡ እናማ…በአደባባይ ‘መሳም’… ‘መታቀፍ’…ፍቅር ላይሆን ይችላል፡፡
የምር…ግራ የሚያጋባ ነገር ነው፡፡ ይቺን አገር የሚያሾሯት ነገሮች “አላዩንም፣ አልሰሙንም…” ተብለው የሚሠሩ ነገሮች መአት ናቸው፡፡ እናማ…በአደባባይ “ተሳምኩ” ተብሎ ከመጋረጃ ጀርባ ‘መነከስ’ አለላችሁ!
አንድ የንግድ ሽርክና ተቋቁሞ ተቃቅፈው ከተለያዩ፣ ሻምፓኝ ከተቃመሱ በኋላ… በአምስተኛ ወሩ ከአምስቱ ሸሪኮች ሦስቱ የ“አላዩንም፣ አልሰሙንም…” የመጋረጃ ጀርባ ‘ግዝገዛ’ ይጀምራሉ። እናማ… ደበቅ ይሉላችሁና ሁለቱን ፈንግለው እንዴት ድርጅቱን እንደሚጠቀልሉ ይመክራሉ፡፡ ግን ምን መሰላችሁ…ቆይቶም ቢሆን ‘ነቄ’ መባሉ አይቀርም፡፡
እናማ ምን መሰላችሁ…ዘንድሮ ብዙ ነገራችን በአደባባይ ‘ጉንጭ ላይ’…ከመጋረጃ በስተኋላ ‘ጀርባ ላይ’ ሆኗል፡፡ የምር ቀሺም ነው…አሀ ልክ ነዋ! በኤድዋርድ ስኖውደን ዘመን “አላዩንም፣ አልሰሙንም…” ብሎ ነገር ቀሺም ነው፡፡
እናላችሁ…ሙሉ ኮሚቴው፣ ሙሉ ሥራ አስፈጻሚ…ምናምን ሳያውቃቸው በ“አላዩንም፣ አልሰሙንም…” የሚተላለፉ ውሳኔዎች መአት ናቸው፡፡ ማለት…በ“አላዩንም፣ አልሰሙንም…” የ‘አባባ ገፋ፣ ገፋ’…‘ታክቲክና ስትራቴጂዎች’ የሚተላለፉ፡፡
እኔ የምለው…የ‘አባባ ገፋ፣ ገፋ’ ነገር ካነሳን አይቀር… እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ይቺን በከተማችን የሆነ ቦታ የተደረገች እውነተኛ ነገር ስሙኝማ፡፡ እናላችሁ…ባልና ሚስቱ የአራት ዓመት ልጅ አላቸው፡፡ ባል ደግሞ ሥራ ነው የሚውለው። ለካስ ሰውየው ሥራ ሲሄድ አንድ መንደር ውስጥ የሚታወቁና ራሳቸውን ‘ሪቻርጅ’ በማድረግ ተወዳዳሪ የሌላቸው ሰው ቤቱ ብቅ ይላሉ፡፡ እናማ… ልጁ “ህጻን ነው፣ አያየንም፣ አይሰማንም…” ብለው እሳቸውና እሜቲት ሚስት ‘እነሆ በረከት’ ምናምን ይባባሉላችኋል፡፡
አንድ ቀን ታዲያ “አያየንም፣ አይሰማንም…” የተባለው ልጅ እየተኮላተፈ ለአባቱ የሰውየውን ስም እየጠቀሰ “አባዬ፣ አንተ ሥራ ስትሄድ አባባ…..ቤታችን ይመጣሉ” ይላል፡፡ አባትየውም ሰውየው መጥተው ምን እንደሚሠሩ ይጠይቀዋል፡፡ ልጁ ምን አለ መሰላችሁ…“ከእማዬ ጋር ገፋ…ገፋ…ገፋ….ያደርጋሉ፣” ሲል ይመልሳል፡፡ የእንቅስቃሴውንም አይነት ለአባቱ በሚችለው መልኩ ያሳያል፡፡
እናላችሁ… ወሬው መንደር ውስጥ ተዛመተና ሠፈርተኛው መካካል የሰውየው መጠሪያ ማን ሆነ መሰላችሁ…“አባባ ገፋ፣ ገፋ…” አሪፍ አይደል!
እናማ… “እነሱ አያዩም፣ አይሰሙም…” እየተባለ የሚደረገው ‘ገፋ፣ ገፋ’ ሁሉ አንዳችን ባናይ ሌላችን እንደምናይ ይታወቅልንማ!
የባልና ሚስት ነገር ካነሳን ይቺን ስሙኝማ…ባል ሆዬ ሚስቱ በሆነ ባልሆነው እየጨቀጨቀችው ለካስ ነገረ ሥራዋ ‘አፍንጫው ጫፍ’ ደርሶበታል፡፡ ታዲያላችሁ…አንድ ቀን እሷ ለቁርስ እንቁላል እየጠበሰች እያለ ማብሰያ ቤት ዘው ብሎ ይገባና ጮክ ብሎ ትዕዛዞች መስጠት ይጀምራል፡፡ “ተጠንቀቂ… ተጠንቀቂ! ትንሽ ቅቤ ጨምሪበት! ኧረ በእግዜሐር! ይሄን ያህል እንቁላል ለምን ጨመርሽ! ያንን ያህል ቅቤ ከየት እናመጣለን! ይጣበቅብሻል ነው እኮ የምልሽ! ተጠንቀቂ… ተጠንቀቂ! ተጠንቀቂ እያልኩሽ እኮ ነው! ምግብ ስታበስይ እኔን አታዳምጪኝም! ሁልጊዜም አታዳምጪኝም! እንቁላሉን ገልበጥ፣ ገልበጥ አድርጊው እንጂ! አንቺ ሴትዮ ነካ ያደርግሻል እንዴ! ያምሻል! ደግሞ ጨው አታብዢ፡፡ ሁልጊዜ ነው እንቁላል ስትጠብሺ ጨው የምትሞጅሪው! ጨው ጨምሪ! ጨው!”
ይሄን ጊዜ ሚስት ብው ትላለች፡፡ “አንተ ሰውዬ ያምሀል እንዴ! እኔ እንቁላል መጥበስ ያቅተኛል!” ብላ ትጮህበታለች፡፡
ባል ሆዬ ምን አለ መሰላችሁ…“መኪና ስነዳ አጠገቤ ሆነሽ ስትጨቀጭቂኝ የሚሰማኝን ስሜት እንድታውቂው ነው!” አለና አረፈው፡፡
እናማ…በየመሥሪያ ቤቱ እነኚህ የፈረደባቸው ‘ዓላማና’…. ‘ግብ’ ምናምን የሚሉ ነገሮች ግድግዳ ሙሉ ተጽፈው ታያላችሁ፡፡ ታዲያላችሁ…ሁሉም ላይ ደግሞ ‘ግልጽነት’ የምትለዋ ነገር አትጠፋም፡፡ ያው እኛም እያየን “ድንቄም ግልጽነት!” እንላለን፡፡ የ“አባባ ገፋ፣ ገፋ…” ዘመን ነዋ!
እዚህ አገር “አያዩንም፣ አይሰሙንም…” ሳይባል የሚሠራ ነገር ምን መሰላችሁ…መንገድ ላይ ፊኛ ማቃለል! የምር…አሳፋሪ ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ አሀ…ጥግ መፈለግ፣ ከግንብ ጀርባ መዞር ምናምን ቀረ እኮ! (አንዳንዴም እነኚህ ነገሮች ከመረሳታቸው የተነሳ… “ጎጂ ባህል…” ምናምን የተባሉ አይመስላችሁም!) በአደባባይ መጸዳዳት ትክክል አለመሆኑን ለልጆቹ ማስተማር የሚገባው ‘ሱፍ በከረባት ግጥም’ ያደረገው ሰው በጠራራ ጸሀይ ትራፊክ መብራት ላይ ዚፕ ሲፈታ ታገኙታላችሁ፡፡ እናላችሁ… አስቸጋሪ ሁኔታዎች እያየን ነው፡፡ አንዳንዴ ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…ከተማዋ በሙሉ ሳንቲም ሳይከፈልባት እንትን መባያ የሆነች ይመስለኛል፡፡
እናላችሁ…በፊት ለፊት ግጥም አድርገን ከሳምን በኋላ ዘወር ሲልሉን ምላሳችንን የምናወጣ አይነት ሰዎች እየበዛን ስንሄድ አሪፍ አይደለም፡፡ እናማ…እንዲህ፣ እንዲህ ሆነን እንዴት መግባባት እንደምንችል…አስቸጋሪ ነው፡፡
ስሙኝማ…የመስማት ነገር ካነሳን አይቀር…ይቺን ስሙኝማ… ሰውየው ምን አለ መሰላችሁ…“ሽማግሌዎቹ ምን ጊዜም ሰርግ ላይ ሲያገኙኝ አጠገቤ ሆነው ጎኔን ነካ ያደርጉና ‘ቀጥለህ አንተ ነህ’ እያሉ ይጨቀጭቁኛል፣” ይላል፡፡
እሱ ምን እንደሚያደርግ ሲጠየቅ ምን አለ መሰላችሁ…“እኔ ደግሞ ቀብር ላይ አጠገባቸው እሆንና ጎናቸውን ነካ እያደረግሁ ‘ቀጥሎ እርሶ ነዎት’ እላቸዋለሁ፡፡”
እናማ…“አያዩንም፣ አይሰሙንም” እየተባለ የሚደረጉ ‘አባባ ገፋ፣ ገፋ…’ ነገሮችን የሚያስቀር ተአምር አንድዬ ይላክልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

ግን ደንታችን አይደለም፤ ነጋዴዎችን ከማውገዝ ለአፍታም አንቆጠብም!

ታዋቂዋ የኢኮኖሚክስ ምሁር ዶ/ር ኢሌኒ ገብረመድህን በእህል ገበያ ዙሪያ ከ20 አመት በፊት ባደረጉት ሰፊ ጥናት የተገኘውን ውጤት በድጋሚ የሚያረጋግጥ አዲስ ጥናት ሰሞኑን በተካሄደው የኢኮኖሚክስ ባለሙያዎች ማህበር ኮንፈረንስ ላይ ቀርቧል። ከጥናቶቹ ውስጥ ጎልቶ የሚታይ አንድ ሃቅ ቢኖር፣ በእህል ገበያ ላይ የተሰማሩ ነጋዴዎችና ደላሎች በየፊናቸው ወይም ተመካክረው እንዳሻቸው የዋጋ ንረትን እንደማይፈጥሩ ነው። እንዲያውም፣ ነጋዴዎች የዋጋ ንረትን የሚፈጥርና ጉዳት የሚያደርስ ቅንጣት ያህል አቅም እንደሌላቸው ጥናቶቹ ያስረዳሉ። እንዲህ አይነቱ ሃሳብና መረጃ የማይዋጥላቸው ብዙ ኢትዮጵያውያን፣ ከገበሬ እህል ገዝቶ የሚያመጣ ነጋዴ ከደላላ ጋር ሆኖ፣ ያሰኘውን ያህል ዋጋ እየጨማመረ በሰፊ ልዩነት የሚሸጥ ይመስላቸዋል።

ከገበሬ የሚገዛበት ዋጋ ከወለል በታች በጣም ዝቅተኛ፣ ለሸማች የሚሸጥበት ዋጋ ደግሞ ከጣሪያ በላይ ከፍተኛ ነው ብለው ያምናሉ። ነጋዴው በሰፊ የዋጋ ልዩነት እጥፍ ሲያተርፍ፣ ከዚያም አልፎ የእጥፍ እጥፍ ዋጋ እየጨመረ ትርፍ ሲዝቅ በምናብ ይታያቸዋል። በተጨባጭ መረጃዎች እና በዝርዝር ጥናቶች ተደጋግሞ የተረጋገጠው እውነታ ግን የዚህ ተቃራኒ ነው። ነጋዴዎች ከገበሬ እህል የሚረከቡበት ዋጋ እና ለሸማች የሚሸጡበት ዋጋ ሲነፃፀር፣ በሁለቱም መካከል ሰፊ ልዩነት እንደሌለ ጥናቶቹ ከመግለፃቸውም በተጨማሪ፣ የዋጋ ልዩነቱ ከአመት አመት በእጅጉ እየቀነሰ መምጣቱን ያስረዳሉ። ታዲያ በእነዚህ ጥናቶችና መረጃዎች ምክንያት የአብዛኛው ሰው አስተሳሰብ የሚቀየርና በነጋዴዎች ላይ የሚሰነዘረው ውግዘት የሚረግብ እንዳይመስላችሁ። ቀድሞውንም፣ በጥናቶችና በመረጃዎች እጦት አይደለም ነጋ ጠባ ነጋዴዎች ላይ የእርግማን ዶፍ የሚዘንበው። በአብዛኛው የአገራችን ሰው፣ ነጋዴዎችን በክፉ የጥላቻ አይን መመልከት ይቀናዋል።

የጥናትና የመረጃ ክምር እየተደራረበ ተራራ ቢያክል እንኳ፣ ብዙ ሰው ከዚህ ጭፍን ጥላቻ ፍንክች ለማለት ፈቃደኛ አይደለም። ለነገሩማ፣ ነጋዴዎች የዋጋ ንረት አለመፍጠራቸውኮ… አዲስ የጥናት ግኝት አይደለም። ሁላችንም በየተሰማራንበት የሥራ መስክ ሁሉ፣ በእለት ተእለት ኑሯችን ዘወትር የምንናየው እውነታ ነው። መቼም፣ በአንዳች ምክንያት እቃ የሸጣችሁበት አጋጣሚ ይኖራል። ወይም ለምትሰሩት ነገር ክፍያ የተደራደራችሁበትን ጊዜ አስታውሱ። በተጨባጭ ያየነው ገጠመኝና በእውን የምንመራው ኑሮ ላይ ተመስርተን ጉዳዩን ስንመረምረው፣ የንግድና የግብይት ጉዳይ ያን ያህልም ውስብስብ አይደለም። በቃ!... ከገበያው ውጭ እንዳሻን የሸቀጦችን ዋጋ ወይም የአገልግሎቶችን ክፍያ ማናር እንደማንችል እናውቃለን። እንዲያም ሆኖ፣ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ነጋዴዎችን በጅምላ እንደ አጭበርባሪ የመቁጠር አባዜ ስለተጠናወተው፣ በተለይ የዋጋ ንረት በተከሰተ ቁጥር ነጋዴዎች ላይ እርግማን ለማውረድ ይሽቀዳደማል።

የተለመደ ነገር ነዋ። ይህም ብቻ አይደለም። የዋጋ ንረት ዋና መንስኤ ምን እንደሆነ ይታወቃል። የዋጋ ንረት የሚፈጠረው፣ መንግስት በገፍ እያተመ በሚያሰራጫቸው የብር ኖቶች ሳቢያ እንደሆነኮ እልፍ መረጃዎችና የሙያው አጥኚዎች በተደጋጋሚ ይመሰክራሉ። መንግስትም አልፎ አልፎ ተጠያቂነቱን በግልፅ አምኖ ሲቀበል ሰምተናል። እንዲያም ሆኖ፣ በኑሮ ውድነት የሚማረር አብዛኛው ዜጋ፣ በነጋዴዎች ላይ የቀሰረውን ጣት ለመመለስ አይፈልግም - ባህላችን ነዋ። … ይቅርታ! የጥናቶቹን ፍሬ ነገር በጨረፍታ ብቻ ጠቅሼ፣ ወደ አስተያየት ገባሁ። ግን፣ ችግር የለም። የጥናቶቹን ዋና ዋና ፍሬ ነገሮች አጠር አጠር አድርጌ መዘርዘሬ አይቀርም። እንዲሁ ሳስበው፣ ከጥንት እስከዛሬ በነጋዴዎች ላይ የሚዥጎደጎደው የማያባራ ውግዘትና እርግማን ስለሚገርመኝ ነው።

እስቲ አስቡት። “በመሰለኝ፣ አሰኘኝ” ስሜት የሚለፈፉ አሮጌ ዲስኩሮችን ዘላለሙን እየመላለስን ከምናመነዥክ፤ እስቲ ለአፍታ ያህል እውነታውን አስተውለን ለማሰብ ለማሰላሰል እንሞክር። በተጨባጭ መረጃዎች ላይ የተመሰረቱት ጥናቶች ውስጥ ተደጋግማ የተገለፀች አንዲት መረጃ ብቻ መዝዤ ልጥቀስላችሁ። የእህል ነጋዴዎች የተጣራ ትርፍ ምን ያህል ይመስላችኋል? ከጠቅላላ የሽያጭ ገቢ ውስጥ፣ ነጋዴዎቹ በአማካይ የሚያገኙት የተጣራ ትርፍ ከ5% በታች እንደሆነ ጥናቶቹ ያረጋግጣሉ። የአንድ ሺ ብር እህል ከሸጠ፣ የተጣራ ትርፉ ከ50 ብር በታች ነው። ተጨማሪ ትርፍ ለማግኘት ለምን ዋጋ አይጨምርም? አይችልማ። ከግራ እና ከቀኝ፣ ከፊትና ከጀርባ ተፎካካሪዎች ከበውታል። እንዳሰኘው የእህል ዋጋዎችን ማናር አይችልም። ጥናቶቹ ይህን እውነታ በግልፅ ቢያሳዩም፤ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ግን እንደወትሮው ነጋዴዎችን ከማውገዝ ወደ ኋላ አይልም። ‘ተምሯል’ የሚባለው የአገራችን ሰውም በአመዛኙ፣ ከልማዳዊው ቅኝት የፀዳ አይደለም። በተጨባጭ መረጃዎች ላይ የተመሰረቱትን ጥናቶች ባነበበ ማግስት፣ ያነበባቸውን መረጃዎች ከአእምሮው ያስወጣቸዋል፤ (ቃል በቃል መረጃዎቹን ከአእምሮው ውስጥ ማስወጣት እንኳ አይችልም። ግን በአእምሮው ውስጥ ብቅ ብርት እያሉ እንዳይታዩት ያዳፍናቸዋል)።

መረጃዎቹን “አውቆ ይረሳቸዋል” ብንል ይሻላል። እናም እንደ ተራው ሰው ሁሉ፣ አብዛኛው ምሁርም ምንም ያህል ጥናት ቢቀርብለት፣ ከጥንታዊው አስተሳሰብ ለመላቀቅ ፈቃደኛ አይደለም። እንደተለመደው ነጋዴዎችን እያወገዘ ይቀጥላል። የኋላቀርነት ባህል በቀላሉ አይነቀልም። ለሺ አመታት የዘለቀውና ስር የሰደደው የአገራችን ባህል፣ ለቢዝነስና ለንግድ ክፉ ጥላቻ አለበት። በኋላቀርነትና በድህነት ውስጥ እንደጨቀየን ለመኖር የተገደድነውም በዚሁ ባህል የተነሳ ነው። ስኬትን በሚጠላ ባህል ከድህነት መውጣት አይቻልማ። ለማንኛውም በመስኩ ባለሙያዎች ዘንድ ሊስተባበሉ ያልቻሉ ሦስት ጥናቶችን ነው የምጠቅስላችሁ። እስካለፈው አመት ድረስ የ25 ዓመታትን የእህል ገበያ ከሚዳስሱት ጥናቶች መካከል የመጀመሪያው፣ ኢትዮጵያዊ ምሁር ከውጭ አገር ባለሙያዎች ጋር በጋራ በሚቺጋን ዩኒቨርስቲ ትብብር ያካሄዱት ጥናት ነው። ምሁራኑ፣ ከ1979 እስከ 88 ዓ.ም ድረስ በአገራችን የእህል ገበያ ውስጥ የአስር አመት መረጃዎችን በማሰባሰብ ጥናት ለማድረግ የወሰኑት አለምክንያት አይደለም። ሁለት የኢኮኖሚ ስርዓቶችን ለማነፃፀር ነበር ፍላጎታቸው። የመጀመሪያዎቹ አራት አመታት የደርግ አገዛዝን ወቅት የነበረውን የእህል ገበያ የሚዳስሱ ናቸው። ገበያው፣ ስፍር ቁጥር በሌላቸው የመንግስት ቁጥጥሮችና ገደቦች፣ በዋጋ ተመኖችና በኬላዎች፣ በኮታና በራሽን ቢሮክራሲዎች የተተበተበ ነበር። ያው፣ “ህብረተሰቡ በአጭበርባሪና በስግብግብ ነጋዴዎች እንዳይበዘበዝ መንግስት ሰፊ ቁጥጥር ማድረግ አለበት” የሚባልበት ዘመን ነው። በዚህ አስተሳሰብም፣ የእህል ገበያው በመንግስት ቁጥጥር እንዲተበተብ ተደርጓል። ቀጣዮቹ 6 አመታት ደግሞ ከደርግ ውድቀት በኋላ፣ በኢህአዴግ ዘመን የእህል ገበያው ሙሉ ለሙሉ ባይሆንም በከፊል ከመንግስት ቁጥጥሮች ነፃ እንዲሆን የተደረገባቸው አመታት ናቸው።

እና የመንግስት ቁጥጥሮችና የዋጋ ተመኖች በከፊል ሲሰረዙ፣ “ስግብግብ ነጋዴዎች” ነፃነት አገኘን ብለው የእህል ዋጋ እንዲንር አደረጉ? አጥኚዎቹ ምሁራን በበርካታ ከተሞች የአስር አመታት መረጃዎችን በማሰባሰብ ያቀረቡት ትንታኔ፣ ነፃ ገበያ በተወሰነ ደረጃ ሲስፋፋ የእህል ዋጋ ንረት እንደሚቀንስ ያሳያል (Jayne, Negassa, Myers. 1998. The effect of liberalization on grain prices and marketing margins in Ethiopia. MSU International Development Working Paper No. 68. Michigan State University)። ከጥናቱ ውስጥ አንድ ምሳሌ ልጥቀስላችሁ። በደርግ ዘመን ሻሸመኔ ላይ ከገበሬ በ66 ብር ተገዝቶ የሚመጣ በቆሎ፣ አዲስ አበባ ውስጥ በ100 ብር ይሸጥ ነበር። በመጣበትና በተሸጠበት ዋጋ መካከል ያለው ልዩነት (marketing spread) 34 በመቶ ነው። ታዲያ፣ የትራንስፖርት፣ የመጋዘን፣ የማውረጃና የመጫኛ፣ ገዢና ሻጭ ለሚያገናኙ ደላሎች ሁሉ ወጪውን ሸፍኖ ነው፣ ነጋዴው በዚህ ዋጋ የሚሸጠው። በመንግስት ቁጥጥር በተተበተበው ገበያ ውስጥ ሸቀጦችና እያመጡ መስራት ብዙ ጣጣና ወጪ ነበረበት። የእህል ገበያው፣ በከፊል ከመንግስት ቁጥጥር ነፃ ሲሆንስ? በ1988 ዓ.ም የእህል ገበያ፣ ሻሸመኔ ውስጥ ገበሬው በ70 ብር ያስረከበው በቆሎ አዲስ አበባ ውስጥ በ90 ብር ገደማ ነው ሲሸጥ የነበረው።

በማምጫና በመሸጫ ዋጋ መካከል ያለው ልዩነት ቀድሞ ከነበረው እየቀነሰ ከ22% በመቶ የማይበልጥ ሆኗል ማለት ነው። ነጋዴው፣ ለምን እንደቀድሞው ዋጋውን ከፍ አድርጎ በመቶ ብር አይሸጠውም? ለሸማቾች አዝኖ አይደለም። በተፎካካሪ ነጋዴዎች ስለተከበበ፣ ሸማቾችን መሳብ የሚችለው በገበያ ዋጋ ተወዳድሮና የተቻለውን ያህል ዋጋ ቀንሶ የሚሸጥ ከሆነ ብቻ ነው። በአጭሩ፣ ነጋዴዎች በአጭበርባሪነትና በስግብግብነት እየተወገዙ መንግስት በስፋት ቁጥጥር እያካሄደ በነበረበት ዘመን አዲስ አበባ ውስጥ በመቶ ብር እንገዛው የነበረ ሸቀጥ፣ ነጋዴዎች ላይ ቁጥጥር እየላላ ሲመጣ ዋጋው ወደ ሰማኒያ ብር ወርዷል።

ለምሳሌ ያህል፣ በበቆሎ ንግድ የሻሸመኔንና የአዲስ አበባን ገበያዎችን ሁኔታ የሚያመላክት ምሳሌ ጠቀስኩላችሁ እንጂ፣ የምሁራኑ ጥናት በርካታ ከተሞችን ያካለለ ነው። መደምደሚያው ግን ተመሳሳይ ነው። የመንግስት ቁጥጥር ሲበራከት ዋጋ ይጨምራል፤ ቁጥጥሮች እየላሉ ነጋዴዎች በነፃነት የሚሰሩት ሁኔታ እየተስፋፋ ሲመጣ ደግሞ ዋጋ ይቀንሳል። ታዲያ፣ ነጋዴዎችን ምን ብንላቸው ይሻላል? “ያልተዘመረላቸው ጀግኖች” እንበላቸው? “ያልተወደሱ ቅዱሳን” ብንላቸውስ ይበዛባቸዋል? ይሄ ለብዙዎቻችን የሚዋጥልን አይደለም። እንዲያውም፣ ማንም ባለሙያ የፈለገውን ጥናት ቢያካሂድ፣ ብዙዎቻችን እንደተለመደው ነጋዴዎችን ከማውገዝና ከመኮነን ለመቦዘን ፈቃደኞች አይደለንም። ዶ/ር ኢሌኒ ገብረመድህን በ1994 ዓ.ም ወዳሳተሙት ሌላ ጥናት እንሸጋገር። ቀደም ካሉት የእህል ገበያ ጥናቶች ሁሉ በላቀ ጥልቀትና ስፋት የተካሄደው የዶ/ር ኢሌኒ ምርምር፣ አገሪቱን ከዳር እስከ ዳር ያዳረሰ፣ ከጤፍ እስከ በቆሎ በርካታ የእህል አይነቶችን የዳሰሰ ከመሆኑም በተጨማሪ፣ ከገበሬ እስከ ደላላ፣ ከጅምላ ነጋዴ እስከ ቸርቻሪ የገበያውን ተዋናዮች በብዛት ይፈትሻል።

ገበሬው የእህል ምርቱን ለገበያ የሚያቀርብበት ዋጋ እንዲሁም፣ ከተሞች ውስጥ በጅምላ አከፋፋዮች በኩል አልፎ በቸርቻሪዎች ለሸማች የሚሸጥበት ዋጋ በንፅፅር ሲታይ ልዩነታቸው ምን ያህል ነው? ከዶ/ር ኢሌኒ ጥናት የተገኘው ውጤት እንደሚያመለክተው፣ በ1988 ዓ.ም በነበረው የእህል ገበያ ውስጥ፣ ገበሬዎች በአማካይ በ78 ብር የሚሸጡት እህል፣ በከተሞች ገበያ ለሸማቹ በመቶ ብር ይቀርብ ነበር። በሁለቱ ዋጋዎች መካከል ያለው ልዩነት 22 በመቶ ነው። ከእያንዳንዷ መቶ ብር ውስጥ፣ ገበሬው 78 ብር ይወስዳል። 22 ብሯስ? ሰባት ብር ለትራንስፖርት ወጪ ይሆናል። ከዚያ በኋላ የምትቀረው 15 ብር ደግሞ፤ ደላሎች፣ አከፋፋዮችና ቸርቻሪዎች፣ ጫኝና አውራጆች፣ ተላላኪና የግብይት ረዳቶች ይከፋፈሏታል። በአማካይ የግብይት ረዳቶችና ተላላኪዎች አምስት ብር ሲወስዱ፣ የደላሎች ድርሻ አንድ ብር ነው። የጆንያ፣ የማደሪያ፣ የመጋዘን ወጪ ወደ 4 ብር ይጠጋል። ስንት ቀረ? አምስት ብር ብቻ። ከዚህች አምስት ብር ነው ለአከፋፋዮችና ለቸርቻሪዎች ትርፍ የምትደርሳቸው። በዶ/ር ኢሌኒ ሰፊ ጥናት መሰረት፣ ከገበሬ እጅ ወጥቶ ሸማች እጅ ውስጥ እስኪገባ ባለው ሂደት ላይ ሁሉ፣ ከመቶ የሽያጭ ገቢ ውስጥ የነጋዴዎች ትርፍ ከ5 ብር አይበልጥም። እናላችሁ፣ የእህል ንግድ የዚህን ያህል ከባድ ስራ ነው። የእህል ነጋዴዎች ከአምስት በመቶ ባነሰ ትርፍ እንደሚሰሩ በጥናት መረጋገጡ፣ ለኛ ምናችን ነው? “በእጥፍ ላይ እጥፍ ዋጋ እየጨመሩ ይመዘብሩናል” እያልን እንደተለመደው ነጋዴዎችን ከማውገዝ አናርፍም! በመጨረሻ ሰሞኑን በኢኮኖሚክ ባለሙያዎች ማህበር አመታዊ ጉባኤ ላይ ከቀረቡት ጥናቶች ላይ አንዱን ላካፍላችሁ።

በአለማቀፍ የምግብ ፖሊሲ ጥናቶች ተቋም እና በኢትዮጵያ የልማት ጥናቶች ተቋም ትብብር በአራት ባለሙያዎች የተካሄደ ጥናት ነው (Ethiopia’s value chains on the move: The case for teff)። በጤፍ ምርትና ግብይት ላይ ያተኮረው ይሄው ጥናት፣ ዘንድሮ በስፋት የተሰበሰቡ መረጃዎችንና ከአስር አመት በፊት የነበረውን ሁኔታ በማነፃፀር ያቀርባል። በ1992 ዓ.ም ገበሬዎች የጤፍ ምርታቸውን በሚያስረክቡበት ዋጋና ነጋዴዎች ለሸማች በሚሸጡበት ዋጋ መካከል የነበረው ልዩነት 22% ገደማ እንደነበር ጥናቱ ይጠቅሳል - የትራንስፖርት፣ የማስጫኛና የማውረጃ፣ የደላላ ወጪዎች እንዲሁም የአከፋፋዮችና የቸርቻሪዎች ትርፍ በዚህ ውስጥ ይካተታል። ከአስር አመት በኋላስ፣ የነጋዴዎች ድርሻ ጨመረ ወይስ ቀነሰ? በገበሬዎች ማስረከቢያ ዋጋ እና በነጋዴዎች መሸጫ ዋጋ መካከል የነበረው ልዩነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰ፣ በአምናው የጤፍ ገበያ ውስጥ እስከ 15% እንደወረደ ጥናቱ ያረጋግጣል። ከገበሬ በ85 የተገዛ እህል፣ ነጋዴዎች ለሸማች በመቶ ብር ይሸጣሉ ማለት ነው - ለዚያውም የደላሎችና የረዳቶች፣ የትራንስፖርትና የጫኝ አውራጅ ወጪዎችን ሁሉ ሸፍነው። እውነታው እንዲህ ከሆነ፣ ከምን ተነስተን ነው ነጋዴዎችን ቀን ከሌት የምናወግዘው? በቃ፣ ነጋዴዎችን መጥላት ባህላችን ስለሆነ፣ ነጋዴዎችን ከማውገዝ አናርፍም። ለመረጃና ለጥናት ደንታ የለንም።

ባሳለፍነው ሳምንት የሻቃ ሀይሌ ገ/ስላሴን ፕሬዚዳንት የመሆን ፍላጐትና ያገኘውን ትኩረት በሚመለከት ከአትሌቱ ጋር ቆይታ ማድረጋችን ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጂ በተፈጠረ ስህተት ቃለ-ምልልሱ ሙሉ ለሙሉ አልቀረበም፡፡ ለተፈጠረው ስህተት አንባቢያንን ይቅርታ እየጠየቅን ሳምንት የቀረውን ቀጣይ ክፍል እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

ሀይሌ አለም አቀፍ ሰው ነው ከፍተኛ እውቅናም አለው ነገር ግን አሁን ሩጫ የሚያቆምበት ዘመን ስለሆነ ላለመረሳት ነው ወደ ፖለቲካው ለመግባት የሰበው ይባላል እውነት ነው?
አቤት አቤት! (በግርምት ጭንቀላቱን እያወዛወዘ) አንድ ነገር ልንገርሽ እኔ እንዳልረሳና ዘላለም እየታወስኩ እንድኖር ከፈለግኩኝ ኢንተርናሽናል ኦሎምፒክ ኮሚቴ ውስጥ ተወዳድሬ መግባት እችላለሁ፡፡ ጓደኛዬ ፖልቴርጋት አሁን እዚያ ሊገባ ነው፡፡ ለዚህ ጥያቄ ከዚህ በላይ ማብራሪያ መስጠት አልፈልግም በቂ ነው፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ እየተከፈለኝ እዚያ መስራት እችል ነበር በቃ ይሄው ነው፡፡
ቀደም ሲል ልጆቼ ሲቪክ ስለሚማሩ ፕሬዚዳንትና ጠቅላይ ሚኒስትር እንዴት እንደሚመረጥ ያውቃሉ ብለሀል ይሁን እንጂ ሃይሌ ልጆቹ አማርኛ መናገር በማይችሉበት ሁኔታ እንዴት አገር ልምራ ይላል የሚሉ አሉ ምላሽህ ምንድነው?
እንዴት ያለ ነገር ነው በናትሽ እንደው በአሉ አሉ ወሬ ስንቱ ገደል ገባ መሰለሽ፡፡

በነገራችን ላይ የኔ ልጆች ይህንን ነገር አለ የተባለው ሰው ጋር ልካተገናኘን ሞተን እንገናኛለን አሉ፡፡ “እሱ እና እኛ ቁጭ ብለን የትኛችን አማርኛ እንደምንችል እንተያይ” ብለው ነበር፡፡ አንድ መጽሔት ላይ ነው ይህ የተፃፈው፡፡ እና እኔ እንዴት እንዳስቆምኳቸው ታውቂያለሽ ይሄ እኮ የቀልድ መጽሔት ነው በቃ ጆክ ነው ብዬ ነው ያሳመንኳቸው፡፡ በነገራችን ላይ በእኔ እምነት አማርኛ ማወቅና አለማወቅ የኢትዮጵያዊነት መገለጫው አይደለም፡፡ እንግሊዝኛ ማወቅም ምሁርነት አይደለም፡፡ እኔ በልጆቼ ከምረካባቸው ነገር አንዱ አገራቸውን መውደዳቸው ነው፡፡ ሁለቱ ትልልቆቹ የ15 እና የ13 ዓመት ናቸው፡፡ (ቢሮው ግድግዳ ላይ ወደተሰቀለው የልጆቹ ፎቶ እያመለከተ) አሁን አንድ ትምህርት ስላላቸው አሜሪካ ነው ያሉት፡፡ አሁን ደውዬ ባሰማሽ “ወደ ኢትዮትያ የምንመለስበት ጊዜ አይደርስም እንዴ” ነው የሚሉት ትላንትና ማታ ለ30 ደቂቃ ነው ያዋራኋቸው ከሄዱ ገና ሁለት ሳምንታቸው ነው፡፡ ይታይሽ እና አንዳንድ ጊዜ መፃፍ ቻልን መድረክ አገኘን ብለው ሃላፊነት የጐደለው ስራ ባይሰሩ ደስ ይለኛል፡፡ የግል አስተያየት በቃ የግል ነው፡፡ ወደ አድማጭና አንባቢ ሲደርስ የሚያመጣውን ችግር መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡
ነገሩ የገጠመበት ደግሞ ምን መሰለሽ ሃዋሳ ላይ አንድ ኢንተርቪው ነበረን፡፡ እኔ እየተጠየቅኩ ሳለ በመሃል ሁለቱ ልጆቼ መጡ፡፡ ደንግጠው የሚሉት ሲጠፋባቸው እንግሊዝኛ እየቀላቀሉ ሲያወሩ በቴሌቪዢን ስለታዬ ነው እንዲህ የሚባለው፡፡ ግን ልጆቼ ጥሩ ኢትዮጵያዊያን ናቸው፡፡ ዞሮ ዞሮ ሁሉንም እየዞሩ ማስረዳት አይቻልም የቢግ ብራዘሯ ቤቲ ገና ሁሉንም ዞራ ማስረዳት ስላልቻለች እንደውም ነገሩ ወደ ክስ እየሄደባት ነው ከአዲስ አድማስ ከጋዜጣሽ እንዳነበብኩት በነገራችን ላይ አንድም ዕትም ሳያመልጠኝ እገዛለሁ የማነበው ጋዜጣ ነው አዲስ አድማስ፡፡
ሰው ወደ ሃላፊነት ሲመጣ ነገሮች አልጋ በአልጋ አይሆኑም ፕሬዚዳንት ብትሆን ምን ውጣውረዶች የሚገጥሙህ ይመስልሃል?
እሱማ ቻሌንጅ እንደሚገጥመኝ አውቄ እየተዘጋጀሁ ነው፡፡ አሁንም ወደ ቻሌንጁ እየባሁ ነው፡፡ ለምን እንዴት፣ ገብተህ ምን ትፈጥራለህ፣ እያሉ ቤተሰቦቼና ጓደኞቼ በጥያቄ ሲያጣድፉኝ እኮ ይሄ የቻሌንጅ መጀመሪያ ነው፡፡ ወደ ውድድር ውስጥ ስትገቢ ደግሞ በርካታ ቻሌንጆች አሉ፡፡ እንዲህ ታግሰሽና ተዘጋጅተሽም አለመመረጥ ይመጣል፡፡ ከተመረጥሽ በኋላ ሌላ ከፍተኛ ቻሌንጅ አለ፡፡ እኔ ወደ ፓርላማ ልግባ ወይም ፕሬዚዳንት ልሁን ስል ላገልግል እንጂ ልገለገል አይደለም፡፡ ምንድነው የምታገለግለው ካልሽኝ በርካታ ነገሮች አሉኝ ልሠራቸው የማስባቸው፡፡
ወደዚያ እንድትገባ የሚፋፋህና አንገብጋቢ የምትላቸው ጉዳዮች ወይም ፓርላማ ብገባ እቀርፋቸዋለሁ ፕሬዚዳንት ብሆን እልባት እሰጥባቸዋለሁ የምትላቸው ችግሮች ምንድን ናቸው?
በጣም በርካታ ጉዳዮች አሉ፡፡ ለምሳሌ በኢኮኖሚው ላይ ማድረግ ያለብን ነገሮች አሉ፡፡ በስራ አጥነት ላይ ከፍተኛ ሥራ መሠራት አለበት፣ አሁንም ኢትዮጵያ ውስጥ ያለ የኤክስፖርት ከሶስትና ከአራት ቢሊዮን ዶላር ያልዘለለ ነው፡፡ መልካም አስተዳደር ላይ ሁሌ እናወራለን፡፡ ግን መልካም አስተዳደር በአንድ ምሽት የሚመጣ አይደለም፡፡ ሂደት ነው በዚያ ላይ ትኩረት ሰጥቼ እሰራለሁ፡፡ እኛ ኢትዮጵያ ነን እያሰብን ያለነው መካከለኛ ገቢ ያለን ዜጐች ስለመሆን ነው ይሄ እንዴት ይመጣል እነማን ናቸው መካከለኛ ገቢ ያላቸው አገራት እከሌ እከሌ፣ እኔ ብዙ አገሮችን በመጐብኘት ባገኘሁት ልምድ የእነዛን አገሮች የማደግ ምስጢር በአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ላይ ተመስርተን ተግባራዊ በማድረግ ለውጥ ማምጣት ላይ መስራት ይቻላል፡፡ በአጭሩ ለመናገር ወደ ፓርላማ የምገባው ተሞክሮዬን ለማካፈል ነው፡፡ ልምዴን ሳካፍል ግን በፖለቲካም በይው በማህበራዊም በይው በኢኮኖሚው በሁሉም ረገድ ጠቃሚ ነው የሚል እምነት ስላለኝ ነው፡፡ ለምሳሌ ማህበራዊ ነገሮችን እናውራ ቢባል ጠቃሚ ባህል እንዳለን ሁሉ ጐጂም ባህል ሞልቶናል፡፡
ምሳሌ እየጠቀስክ ብትነግረኝ …
ለምሳሌ ኢትዮጵያ ውስጥ እንነጋገር ከተባለ የኢትዮጵያ የሠርግና የሀዘን ሁኔታ አስቸጋሪ ነው፡፡ ሰርጋችንም ሀዘናችንም ከአንድ ሳምንት በላይ ይወስዳል ሰርግም ሀዘንም አያስፈልግም እያልኩ አይደለም በዓላት አከባበር ላይ ብታይ ጊዜ የሚድል ነገር ነው የምታይው ይህ ሁሉ ካልተስተካከለና ጊዜ አጠቃቀማችን ላይ ( ) ካለመድን ለውጥ ማምጣት አይቻልም በዚህ ላይ እሠራለሁ የሚል እምነት አለኝ፡፡ ለዚህ ደግሞ ራሴ ምሳሌ ሆኜ መገኘት አለብኝ፡፡ ሠርቼ ነው ማሳየት ያለብኝ
ሰርግን በተመለከተ ላነሳኸው አንተ በሠርግ ነው ያባኸው መልስም እንደነበረህ አልጠራጠርም በዚህ እንዴት ሌላውን ማስተማር ትችላለህ?
እኔ ሰርጌ የዛሬ 16 ዓመት ነበር፡፡ ሠርግ ነበር ግን ይህን ያህል ቀን የፈጀ አይደለም አላደረግኩትም፡፡ ከሰርጌ በኋላ በማግስቱ ልምምድ ላይ ነበርኩ፡፡ መልስ ሄደሃል ወይ አዎ ሄጃለሁ፡፡ ነገር ግን ልምምድ ሰርቼ ስጨርስ ነው መልስ የሄድኩት፡፡ ይሄው ነው፡፡ እነዚህ እነዚህ ነገሮች ላይ መስራት አለብን፡፡ ይሄ ያሳስበኛል እሠራበታለሁ፡፡
አንተ በግልህ ይህቺን አገር ፕሬዚዳንት ሆኖ ለመምራት አንድ ሰው ምን ምን ነገሮችን ሊያሟላ ይገባል ትላለህ?
ከበርካታ ነገሮች ውስጥ አንቺ ጣል ጣል ያደረግሽው እውቅና ቢኖር ጥሩ ነው፡፡ ካለኝ እውቅና እና እንደ ኢትዮጵያዊ አትሌቲክስ በውጭው ያሉ የአለም መሪዎችን የማግኘት እድል ገጥሞኛል መሪ ስትሆኚ ደግሞ የዛን ሁለትና ሶስት እጥፍ ነው ስለዚህ እውቅና አንዱ ሊሆን ይችላል ማለቴ እውቅና ካለ ያግዛል ግን ግድ አይደለም በተረፈ ዋናው ግን ልምድ “Experience” የሚባለው ወሳኝ ነው፡፡ ለምሳሌ የአሁኑን ፕሬዚዳንት አቶ ግርማን እያቸው ልምዳቸው የትናየት እንደሆነ፡፡ በተለያየ ዘርፍ የካበተ ልምድ አላቸው፡፡ እንዲህ አይነት ሰው ያስፈልጋል በተረፈ አገሪቱን እና ህዝቧን በደንብ ማወቅ ወሳኝ ነው፡፡ አዲስ አበባ ብቻ አይደለችም ኢትዮጵያ የህዝቡን ስነ - ልቦና የዝቅተኛውን ህብረተሰብ ኑሮ ማወቅ መረዳት ለአንድ መሪ ወሳኝ ነው እነዚህን ማሟላት ያስፈልጋል፡፡ በዋናነነት የምትመሪውን ህዝብ ማወቅ አለብሽ ማወቅ ያለብሽ በከፊል ሳይሆን ሙሉ ለሙሉ ነው፡፡ ለሁሉም አባት ሆኖ ነው መሪ የሚመረጠው አንዱ ሀብታም ነው ሌላው ደሀ ነው ያልተማረነው የተማረነው የሚል የለም፡፡ ሁሉንም እኩል ማየት ይጠበቅበታል፡፡ ይህን ሁሉ የምነግርሽ የእኔ የራሴ የግሌን አስተያየት ነው፡፡
ካነሳሀቸው ሀሳት አንፃር አንተ እነዚህን ጉዳዮች አሟላለሁ ብለህ ታስባለህ በእውቅናስ ብቻ አገር ይመራል የሚል እምነት አለህ?
እሱማ እግር ነቃ ማለት ጭንቅላት ነቃ ማለት አይደለም ነገር ግን የተሻለ የብዙ አገር ልምድ አለኝ ብዬ አስባለሁ፡፡ እውቅና ብቻ ሳይሆን በተዘዋወርኩባቸው በርካታ አገራት የተለያዩ ለአገር የሚበጁ ልምዶችን አካብቻለሁ መስፈርቶቹን ከሞላ ጐደል አሟላለሁ የሚል እምነት አለኝ፡፡
አሁን ስንት አመትህ ነው
አርባ አመት ሞላኝ
እድሜም ለመሪነት ወሳኝ ነው አይደለም እንዴ?
በትክክል ወሳኝ ነው አሁን ስለፕሬዚዳንት “ስላወራን ነገ ዘልዬ ፕሬዚዳንት ልሆን አልችልም፡፡ አሁን ፕሬዚዳንት የተዘጋጀ ይመስለኛል ከመስከረም ጀምሮ በአዲስ ፕሬዚዳንት እንመራለን የሚል እምነት አለኝ፡፡ እኔ ፓርላማ እገባለሁ፡፡ አዲሱ ፕሬዚዳንት ስድስት አመት ይመራሉ እስከዛ እኔ ፓርላማ እቆያለሁ እድሜዬም ያን ጊዜ ይታያል፡፡

 

ፕሬዝዳንት የሚሆነው ግለሰብ የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባል ብቻ ስለመሆኑ ወይም ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዕጩ ሆኖ መቅረብ የሚችል ስለመሆኑ ግልጽ ባለ ሁኔታ የተደነገገ አንቀጽ በሕገ መንግስቱ ውስጥ አይገኝም፡፡ ይሁን እንጂ፣ አንቀጽ 70 ንዑስ አንቀጽ 3 እንዲህ ይላል “የምክር ቤት አባል ፕሬዝዳንት ሆኖ ከተመረጠ የተወከለበትን ምክር ቤት ወንበር ይለቃል” ይላል፡፡ ይህ ጥቅል አገላለጽ በውስጡ በርካታ ጉዳዮችን የያዘ ይመስለኛል፡፡

 ሰሞኑን በመዲናችን እየተናፈሱ ካሉት የወሬ ቱማታዎች አንዱ፣ በመጪው መስከረም ወር 2006 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ሆኖ የሚመረጠው ሰው ማን እንደሆነ የመተንበይ ጉዳይ ነበር፡፡ በወሬው ሂደት በፕሬዝዳንትነት ዕጩ ሆነው ይቀርባሉ ከተባሉት ግለሰቦች አንዱ እውቁ አትሌት ኃይሌ ገ/ስላሴ እንደሆነም ተደጋግሞ ሲጠቀስ ሰምተናል፡፡ 

ታዋቂው አትሌት ኃይሌ ገ/ስላሴም ይህንኑ ጉዳይ አስመልክቶ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ የሐምሌ 13 ቀን 2005 ዓ.ም እትም ላይ ቃለ ምልልስ አድርጓል፡፡ አትሌት ኃይሌ “በመጪው ምርጫ ፓርላማ እገባለሁ፤ ግን ወዲያው ፕሬዝዳንት አልሆንም” በሚል የሰጠውን ቃለ ምልልስ ካነበብኩ በኋላ እነሆ ይህቺን ጽሁፍ ለማዘጋጀት ተነሳሁ፡፡
በዚህ መጣጥፍ በሦስት ጉዳዮች ላይ ትኩረት ማድረግን መረጥኩ፡፡ አንደኛ፤ ከሀገሪቱ ሕገ-መንግስት እና ከሁለቱ ምክር ቤቶች (ከሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት እና ከፌዴሬሽን ም/ቤት) የጋራ ስብሰባ መተዳደሪያ ደንብ አኳያ የፕሬዝዳንት አመራረጥን በተመለከተ የፈጻጸም ሂደቱን መቃኘት፣ ሁለተኛ፤ አትሌት ኃይሌ በቃለ ምልልሱ ባነሳቸው አንዳንድ ሃሳቦች ዙሪያ አስተያየት መስጠት እና ሦስተኛ፤ የሀገሪቱ 3ኛ ፕሬዝዳንት ማን ቢሆኑ ይሻላል? በሚለው ላይ የግል እይታዬን ማቅረብ ይሆናል፡፡
የፕሬዝዳንት አመራረጥ፣
ብዙ ሰዎች የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት የሚሆነው ሰው በግሉ ተወዳድሮ በማሸነፍ የፓርላማ አባል የሆነ ግለሰብ ብቻ እንደሆነ ሲናገሩ ይደመጣል፡፡ በዚህ ረገድ ያለውን ብዥታ ለማጥራትና ትክክለኛውን ግንዛቤ ለመያዝ የህገ መንግስቱን ድንጋጌ መመልከቱ ጠቃሚ ይመስለኛል፡፡ በህገ መንግስቱ አንቀጽ 70 ንዑስ አንቀጽ 1 መሰረት ፕሬዝዳንት የሚሆንን ሰው ዕጩ አድርጎ የማቅረብ ስልጣን የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ነው፡፡ ይሁን እንጂ፣ ይህ ዕጩ ፕሬዝዳንት የሚሾመው በሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት እና በፌዴሬሽን ም/ቤት የጋራ ስብሰባ በተገኙ አባላት በሁለት ሦስተኛ (2/3ኛ) ድምፅ ድጋፍ ያገኘ እንደሆነም፣ በአንቀጽ 70 ንዑስ አንቀጽ 2 ላይ ተደንግጓል፡፡ ፕሬዝዳንት የሚሆነው ግለሰብ የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባል ብቻ ስለመሆኑ ወይም ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዕጩ ሆኖ መቅረብ የሚችል ስለመሆኑ ግልጽ ባለ ሁኔታ የተደነገገ አንቀጽ በሕገ መንግስቱ ውስጥ አይገኝም፡፡ ይሁን እንጂ፣ አንቀጽ 70 ንዑስ አንቀጽ 3 እንዲህ ይላል “የምክር ቤት አባል ፕሬዝዳንት ሆኖ ከተመረጠ የተወከለበትን ምክር ቤት ወንበር ይለቃል” ይላል፡፡ ይህ ጥቅል አገላለጽ በውስጡ በርካታ ጉዳዮችን የያዘ ይመስለኛል። እኔ እንደገባኝ ከሆነ፣ የዚህ አንቀጽ መንፈስ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ለፕሬዝዳንትነት እጩ ሆኖ መቅረብ የሚችል መሆኑን፤ ይሁን እንጂ እጩው የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባል ከሆነ (የምክር ቤት አባልም ፕሬዝዳንትም መሆን ስለማይኖርበት) መቀመጫውን እንደሚለቅ ያስገነዝባል፡፡
የዚህን አንቀጽ ትርጉም ሰፋ አድርገው የሚያዩ አንዳንድ ሰዎች “የተወከለበትን ምክር ቤት ወንበር ይለቃል” ማለት የፓርቲ አባል ከሆነ ‘የፓርቲ መታወቂያውን ይመልሳል’ ማለት እንደሆነ አድርገው ሲናገሩም የሰማሁበት አጋጣሚ አለ፡፡ በኔ እምነት ይህ አተረጓጎም ግን ትክክል አይመስለኝም፡፡ ያ ቢሆን ኖሮ የመጀመሪያው የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት የነበሩት ዶ/ር ነጋሦ ጊዳዳ፤ እስከ ስልጣን ዘመናቸው ማብቂያ ድረስ የኦህዴድ አባል ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ አመራርም ሆነው አይዘልቁም ነበር የሚል መከራከሪያ ማቅረብ የሚቻል መስለኛል፡፡ ከላይ የጠቀስኩት የሕገ መንግስቱ ድጋጌ እንተጠበቀ ሆኖ፤ በሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት እና በፌዴሬሽን ም/ቤት የጋራ የአሰራርና የስብሰባ ሥነ-ስርዓት ደንብ ቁጥር 1/2000 ላይ፤ ስለ እጩ ፕሬዝዳንት አቀራረብ፣ አንድ እጩ ፕሬዝዳንት ማሟላት ስለሚገባው መስፈርት፣ ስለ ሌሎችም ጉዳዮችና ዝርዝር የአፈጻጸም ሂደቶች የተብራራበት ሁኔታ አለ፡፡በዚሁ ደንብ አንቀጽ 5 ንዑስ አንቀጽ 3 መሰረት፤በዕጩ ፕሬዝዳንትነት የሚቀርብ ሰው አራት መስፈርቶችን ማሟላት እንዳለበት ተደንግጓል። ይኸውም፤ (1) ለሕገ መንግስቱ ታማኝ የሆነ፣ (2) ሀገሪቱን በርዕሰ ብሔርነት ለመምራት የሚያስችል ብቃትና ሥነ-ምግባር ያለው፣ (3) ዕድሜው 21 ዓመት እና ከዚያ በላይ የሆነ እና (4) ኢትዮጵያዊ ዜጋ የሆነ፣ የሚሉ ናቸው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ “ለፕሬዝዳንትነት እጩ ሆኖ የሚቀርብ ማንኛውም ሰው ከማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት ወገንተኛነት ነፃ ሆኖ ለማገልገል ፈቃደኛ መሆን አለበት” የሚል ድንጋጌ በዚሁ ደንብ በአንቀጽ 5 ንዑስ አንቀጽ 4 ላይ ተደንግጓል፡፡
አንድ ሰው ለሁለቱ ምክር ቤቶች የጋራ ስብሰባ እጩ ፕሬዝዳንት ሆኖ ለመቅረብ ደግሞ በቅድሚያ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስብሰባ በአብላጫ ድምፅ እጩነቱ ተቀባይነት ማግኘትና መጽደቅ እንደሚኖርበትና የዚህ አፈጻጸም ሂደትም በጋራ ደንቡ በአንቀጽ 5 ንዑስ አንቀጽ 1 እና 2 ላይ በዝርዝር ተብራርቷል፡፡
የአትሌት ኃይሌ ቃለ ምልልስ፣
አትሌት ኃይሌ ገ/ስላሴ ከላይ በዝርዝር የጠቀስኳቸውን የሕገ መንግስት እና የሁለቱ ም/ቤቶች የጋራ ስብሰባ መተዳደሪያ ደንብ የፕሬዝዳንት አመራረጥ ድንጋጌዎች ይወቃቸውም አይወቃቸው በመጪው ሀገራዊ ምርጫ ተወዳድሮ በማሸነፍ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል ለመሆን እና ከዚያም የሀገሪቱ ርዕሰ ብሔር ለመሆን መነሳቱ መልካም ነገር ይመስለኛል፡፡ ባደጉትና በሰለጠኑት ሀገሮች የጎላ የፖለቲካ ተሳትፎ የሚያደርጉት ምሁራንና ባለሀብቶች እንደሆኑ ይነገራል፡፡ የሀገራችን ምሁራን፣ ታዋቂ ግለሰቦችና ባለሀብቶች በስልጣን ላይ ያለውን ገዢ ፓርቲ ፖሊሲዎችና አፈጻጸም በሩቁ ሆነው ከመተቸትና ከማማረር አልፈው ወደ ፖለቲካው መድረክ ብቅ ሲሉ ብዙም አይታይም፡፡ እናም በዚህ ረገድ አትሌት ኃይሌ ያሳየው ተነሳሽነት የሚያስመሰግነው እንደሆነ እገነዘባለሁ፡፡
ይሁን እንጂ፣ አትሌት ኃይሌ ወደ ፖለቲካው መድረክ “ዘው” ብሎ ከመግባቱ በፊት በጥልቀት ሊያያቸውና ሊመረምራቸው የሚገቡ ጉዳዮች ያሉ መሆኑን በዚህ ጽሁፍ መግቢያ ላይ በጠቀስኩት አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ከሰጠው ቃለ ምልልስ ለመገንዘብ ችያለሁ፡፡ ለምሣሌ፤ “ፕሬዝዳንት ብትሆን ምን ምን ሥራዎችን እንደምታከናውን ግለጽልኝ” ተብሎ ለቀረበለት ጥያቄ “በስራ አጥነት፣ በመልካም አስተዳደር፣ በኤክስፖርት ላይ ብዙ መስራት ይቻላል…” የሚል መልስ ሰጥቷል፡፡
ይህንን የኃይሌን መልስ ሳነብ፣ አትሌት ኃይሌ ከተራ ሀገር ወዳድነት እና ከሥራ ተነሳሽነት ውጪ “ፖለቲከኛ” የሚያደርገው አቅም የገነባ አለመሆኑን ነው የተረዳሁት፡፡ የፕሬዝዳንቱ የስራ ድርሻ ምን ምን እንደሆነ እንኳ ሕገ መንግስቱን አንብቦ በቅጡ የተገነዘበ አልመሰለኝም፡፡ እንኳን የጠለቀ ግንዛቤ ሳይዙ የመጠቀ ግንዛቤ ተይዞም የኢትዮጵያ ፖለቲካ ዳር ላይ ሆነው እንደሚያዩት ቀላል አደለም፡፡ ሁላችንም እንደምናውቀው በእኛ ሀገር የፕሬዝዳንቱ ስልጣን ውሱን (በእንግሊዝኛው አገላለጽ Ceremonial) ነው፡፡ በሕገ መንግስቱ በተደነገገው መሰረት የፕሬዝዳንቱ የስራ ድርሻ በአጭሩ “በየዓመቱ የሁለቱን ም/ቤቶች የጋራ ስብሰባ በንግግር መክፈት፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሲያቀርቡ አምባሳደሮችን መሾም፣ ፓርላማ ያጸደቃቸውን ሕጎች መፈረምና በነጋሪት ጋዜጣ ማወጅ፣ ኒሻንና ሽልማት መስጠት፣ ይቅርታ ማድረግ፣…ወዘተ.” የሚሉ ናቸው፡፡ በሕገ መንግስቱ ከተሰጠው ስልጣን ውጪ መስራት እንደማይቻልም ይታወቃል፡፡
ይሁን እንጂ፣ አትሌት ኃይሌ ይህንን ባለመገንዘብ ይመስለኛል “ሥራ አጥነትን፣ መልካም አስተዳደርን፣ ጠቃሚ ያልሆኑ ባህሎችን፣ ሰርግን፣… ወዘተ.” የመሳሰሉትን በተመለከተ እሰራለሁ የሚል መልስ በቃለ ምልልሱ ያነሳው፡፡ ልክ በአትሌቲክሱ በማራቶን ለመወዳደር የተመዘገበ፣ በመቶ ሜትር ርቀት መወዳደር እንደማይችለው ሁሉ፣ፕሬዝዳንቱ የጠቅላይ ሚኒስትሩን የሥራ ድርሻ ሊሰራ እንደማይችል ወንድሜ ኃይሌ ልብ አላለውም፡፡
እዚህ ላይ አንድ ነገር ለማለት ወደድሁ፡፡ አትሌት ኃይሌ፣ በአትሌቲክሱ መስክ የተዋጣለት ሥራ በመስራት ስኬታማ ሊሆን የቻለው በመስኩ የጠለቀ እውቀትና ግንዛቤ ያለው አሰልጣኝና ማናጀር በሚሰጠው ምክርና አቅጣጫ በመጓዙ ይመስለኛል። ስለሆነም፤ በፖለቲካውም መስክ የተሳካ ውጤት ላይ ለመድረስ በቂ ግንዛቤና ልምድ ያለው አማካሪ ቢኖረው መልካም ነው፡፡ በዚህ ረገድ እኔን ጨምሮ የቀድሞ የተቃዋሚ ወይም የኢህአዴግ አባል የነበርን “የፖለቲካ ጡረተኞች” ስላለን የአማካሪ ችግር የሚኖር አይመስለኝም፡፡ ባይሆን ከእጅህ ፈታ ማለት ነው - ወዳጄ ኃይሌ! (አጋጣሚውን በመጠቀም አዲስ አድማስ ያላወቀው ማስታወቂያ መስራቴ ነው)
ማን ፕሬዝዳንት ይሁን?
ባለፉት አስራ ስምንት ዓመታት ሁለት ፕሬዝዳንቶች በርዕሰ ብሔርነት ተሹመዋል። አሁን በስራ ላይ ያሉት ፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ የስልጣን ዘመን በመጪው መስከረም ወር 2006 ዓ.ም እንደሚጠናቀቅና አዲስ ፕሬዝዳንት እንደሚመረጥ ይጠበቃል፡፡ እጩ ፕሬዝዳንቱን መርጦ በማቅረብ ረገድ ደግሞ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አብላጫ መቀመጫ ያለው መሪው ፓርቲ ኢህአዴግ ትልቁን ሚና እንደሚጫወትም ይታመናል፡፡ በመስፈርቱ መሰረት ኢህአዴግ ይህንን “እድል” ለማን እንደሚሰጥ ምንም ዓይነት ፍንጭ አልሰማሁም፡፡ ግን ለማን ቢሰጥ ይሻላል? ከፆታ አኳያ ለወንዶች ወይስ ለሴቶች? ከዕድሜ አኳያ ለወጣት፣ ለጎልማሳ ወይስ ለአረጋዊ? ከሃይማኖት አኳያ ለኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ፣ ለሙስሊም፣ ለካቶሊክ፣ ለፕሮቴስታንት ወይስ ለሌላ? ከብሔር ብሔረሰቦች አኳያ ለሶማሌ፣ ለአፋር፣ ለመዠንገር፣ ለሀዲያ፣ ለከንባታ፣ ለኩናማ፣ ለኤሮጵ፣ ለኛጋቶም፣ ለሙርሲ፣ ለሐመር፣…ወይስ? ኢህአዴግ ካለፉት ሁለት የእጩ ፕሬዝዳንት አቀራረቦች ሂደት የተገኙ ተሞክሮዎችን በማየትና ከላይ የጠቃቀስኳቸውን የፆታ፣ የዕድሜ፣ የሃይማኖትና የብሔር ብሔረሰቦች ስብጥር ከግንዘቤ በማስገባት፣ በአንፃራዊነት የኢትዮጵያን ሕዝቦች ሊወክል የሚችል እጩ ቢያቀርብ የተሻለ እንደሚሆን አስባለሁ፡፡ በተለይ ደግሞ ከሀገሪቱ ዜጎች ከግማሽ በላይ ለሚሆኑት ለሴቶች እድሉ ቢሰጥ የተሻለና አስፈላጊም ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ በዚህ ረገድ ይህንን ኃላፊነት ሊሸከሙ የሚችሉ እውቀትም፣ ልምድም ሆነ ችሎታ ያላቸው በርካታ ሴቶች እንዳሉ ቅንጣት ታህል ጥርጣሬ የለኝም፡፡ ከታሪክም አኳያ እንኳን አሁንና በጥንታዊት ኢትዮጵያ እነ ንግስት ሳባ፣ ንግስት እሌኒ፣ ንግስት ሀዲያ፣ ዮዲት ጉዲት (ባኑኤል ሃይሙያ?)፣ ዘውዲቱ እና ጣይቱ የነበራቸውን ሚና ማስታወስ መልካም ነው፡፡

በቅርቡ በደሴ ከተገደሉት የሃይማኖት አባት ጋር ተያይዞ መንግስት በተደጋጋሚ መግለጫዎችን እያወጣ ሲሆን ተቃዋሚዎች በበኩላቸው መንግስት ከሃይማኖት ጉዳዮች እጁን እንዲያወጣ እየጠየቁ ነው፡፡ በሃይማኖትና በአክራሪነት እንዲሁም በተቃዋሚዎች አቋም ዙርያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ከፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተክለማርያም ጋር የሚከተለውን ቃለ ምልልስ አድርጓል፡፡

መንግስት በተከታታይ ከሀይማኖት አክራሪነት ጋር የተያያዙ መግለጫዎችን መስጠቱ ለምን አስፈለገ? ጉዳዩን የበለጠ ማጋጋል አይሆንም?
ጥሩ ነጥብ ነው የተነሳው፡፡ በሃገራችን፣ ሁሉም አይነት የእምነትና ሃይማኖት ችግሮች የተከሰቱባቸው ጊዜያት እንደነበሩ ይታወቃል፡፡ አሁን ከሃይማኖትና እምነት ጋር ተያይዞ ያለንበት ምዕራፍ አዲስ ነው፡፡ እነዚያ ችግሮችም አሁን የሉም ብለን ነው የምናስበው፡፡ ህገ መንግስታችንም የሚለው ይህን ነው፡፡ ባለፉት ሁለት አስርት አመታት መሪ ድርጅቱም ይሁን ተጨባጭ ተግባሩ ይሄው ነው። ይህ እንዳለ ሆኖ ሁላችንም እንደምናውቀው የሃይማኖቶች አብሮ በሰላም ተቻችሎ የመኖር እሴት ያለን ሃገር ነን፡፡ የተዛቡ ግንኙነቶች በህገ መንግስታችን የተስተካከሉበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ እንዲህ አብሮ በሰላም የመኖር እሴት ባለበት ሃገር ላይ የሚመጡ ዝንባሌዎች ሃይማኖታዊ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ በሌላ በኩል ግን የሃይማኖት አጀንዳ በሚነሳበት ጊዜ ሚዛናዊ የሆነ አረዳድ ለመያዝ ሰው ሊቸገር ይችላል፤ ምክንያቱም ከሃይማኖቱ ጋር ተጣብቆ ሊነሳ ስለሚችል፡፡

ትክክለኛ መረጃ ሳይያዝ በእርግጥም በሃይማኖታችን ላይ ያነጣጠረ ሰው አለ የሚል አይነት አዝማሚያና ዝንባሌ ሊፈጥር ይችላል፡፡ አክራሪነት አንዱ ጥቅም ላይ የሚያውለው ይህንን ነው፡፡ ይህ ደካማ ጎን ነው እኛን ወደ ፊት ሊያራምድ የሚችለው የሚል አመለካከት ነው የሚኖረው፡፡ እኛ አክራሪነትና ፅንፈኝነትን ከህገ መንግስታችን ተነስተን ነው የምንፈርጀው ብለናል። ከመፅሃፍት ወይም ከመዝገብ ቃላት ተነስተን አይደለም፡፡ ከዚህ በፊትም ደጋግመን እንደምናነሳው የዜጎችን የእምነት ነፃነት ህገ መንግስታችን ሰጥቷል። እንደዚህ ያልኩት በአንዳንድ ሃገሮች የተወሰኑ ሃይማኖቶች ተዘርዝረው ከዚህ ውጪ የምናውቀው ሌላ ሃይማኖት የለም ይባላል፤ እንዲያም ሆኖ ነፃነት አለ ተብሎ ይወሰዳል። የሃይማኖት እና የእምነት ነፃነት የተከበረና የተጠበቀ ነው ተብሎ ሲባል ዋነኛ መስፈርቱ ሁሉም የሚፈልገውን የኔ ነው የሚለውን እንዲያመልክ ሊፈቀድለት ይገባል፡፡ ተፈጥሮአዊ ስለሆነ እውቅና ሊሰጠው ይገባል፡፡
የአክራሪነትና ፅንፈኝነት ሂደት ግን ከዚህ ተቃራኒ ነው፡፡ እኛ ትክክለኛ ነው ያልነውን ብቻ ከመከተል ያለፈ ሌላ አማራጭ የለም ብሎ የሚዘጋ ነው፡፡ ሌላው የሃይማኖት እኩልነትን መቃረን፣ መንግስታዊ ሃይማኖትን መፈለግ የሚሉት ናቸው፣ የአክራሪነትና የሃይማኖት ፅንፈኝነት ማጠንጠኛ ነጥቦች፡፡
ለምንድነው ተከታታይ መግለጫዎች በሼህ ኢማም ኑር እና በአክራሪነት ዙሪያ ላይ እንዲሰጥ የተፈለገው የሚለውም ይህን ጉዳይ ግልፅ ለማድረግ ነው፡፡ መንግስትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው ሲባል፣ ዜጎች በሃይማኖት ምክንያት በደል ሲፈፀምባቸው ምናልባትም አሁን እንዳየነው አይነት ግድያ ሲፈፀምባቸው ዝም ብሎ ያያል ማለት አይደለም፡፡ መንግስት እንደዚህ አይነት ሁኔታ ሲያጋጥም ህዝቡን መጀመሪያ በደንብ ማስተማር አለበት፡፡ ይህ ጉዳይ ሃይማኖታዊ አይደለም፤ ህገመንግስታችንን የሚጥስ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ስንለው የነበረው በተጨባጭ እየመጣ ነው የሚለውን በተደጋጋሚ መግለጫዎች ማሳየት ከዚህ አንፃር ተገቢ ነው፡፡
እነዚህ አካላት ከኔ ሌላ መኖር የለበትም በሚለው አመለካከታቸው የራሳቸውን ሃሳብ በሌሎች ላይ በግድ ለመጫን የሚንቀሳቀሱ ናቸው፡፡ ይህን ለማስፈፀም ከሚጠቀሙት ስልት አንዱ እንግዲህ የሰሞኑ የሼክ ኢማም ኑሩ ግድያ ማሳያ ነው፡፡ አልፎ ተርፎ መንግስት ነው የገደላቸው እያሉ እያስወሩም ነው፡፡ እንግዲህ ይህ የከፋ ህዝብን የመናቅ ደረጃ ላይ መድረሳቸውን ነው የሚያሳየው፡፡ ህዝቡን በተለይም ለሃይማኖቱ ቀና የሆነውን ወጣቱን ህብረተሰብ እንደፈለግን እናሽከረክረዋለን ከሚለው አመለካከት የመጣ ነው፣ ገድለው ሲያበቁ “ይህን ድራማ የሰራው መንግስት ነው” ያሉት፡፡ መንግስት እዚህ እንካ ሰላንቲያ ውስጥ የሚገባበት ምክንያት የለም፡፡ በማህበራዊ ድረገፆችም ሆነ በተለያዩ መድረኮች ይህ ያልተገባ እንካ ሰላንቲያ እንዲካሄድ እየፈለጉ ነው፡፡ ይህን ብዥታ ለማጥራት ደግሞ… በመንግስት በኩል ህዝባችን ግልፅና የጠራ ግንዛቤ እንዲኖረው ማድረጉ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ጉዳዩን አጉልቶ ማሳየትም አስፈላጊ ነው፡፡
የምናምነው ደግሞ አክራሪነትና ፅንፈኝነት መጨረሻው አሸባሪነት መሆኑን ነው፡፡ ይህንን ነው ስንለው የነበረው፤ በተጨባጭም የታየው ይሄው ነው፡፡ ይህ ደግሞ ሁሉንም ህዝበ ሙስሊምም ሆነ የሀገራችንን ህዝቦች የሚወክል አይደለም፡፡ ዝም ብሎ ቢተውም ድራማውን እውነተኛ አድርገው ማስወራታቸው ስለማይቀር ነው አጉልቶ ማውጣት ያስፈለገው፡፡ ለምንድን ነው መንግስት ልዩ ትኩረት የሰጠው ለሚለውም፣ በጉዳዩ ላይ መንግስትም ሆነ ህገመንግስታዊ ስርዓቱን እጅግ የሚፈታተን ሁኔታ ነው የተፈጠረው፡፡ የህግ የበላይነትንና ህገ መንግስታዊ ስርዓትን የማፃረር ስራ ነው የተሰራው። ህገመንግስታዊ ስርዓታችንን የሚፃረር ስራ በሚሰራበት ጊዜ መንግስት ዝም ብሎ ቀላል አድርጎ ሊያይ አይችልም፡፡
አሁን ሼህ ኢማም ኑሩ የመኖርና፣ በፈለጉት ሴክት የእምነት ክፍል ውስጥ የመሆን መብታቸው ተደፍሯል፡፡ መንግስት እንዲህ አይነት ህገመንግስታዊ የመብት ጥሰት በሚያጋጥምበት ጊዜ፣ የዜጎችን ሰላም የማስጠበቅና ጥቃቶችን የመከላከል ሃላፊነት አለበት፡፡ በአንድ የሃይማኖት ምሁር/አባት/ የተፈፀመው ብቻ አይደለም መታየት ያለበት። በዚህ አይነት መንገድ የተሟላ የህግ የበላይነት ሳይከበር ቢታለፍ፣ የዚህ አይነት ነገሮች ይለመዳሉ። በቁጥጥር ስር የዋሉ ሰዎች እንደገለፁትም፣ በብዙ ሰዎች ላይ ተመሳሳይ ድርጊት ሊፈፀም ሲቀነቀን ነበረ፡፡ በዚህ ዙሪያ ላይ ለህብረተሰቡ የተሟላ መረጃ አቅርቦ፣ በቂ ግንዛቤ ፈጥሮ፣ ህዝቡ በደንብ ተወያይቶ፣ ትክክለኛው መደምደሚያ ላይ መድረሱ እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡
እንደዚህ ጉዳይ ለምን ይጦዛል የሚሉ አካላት ሁለት አይነት መልክ ይኖራቸዋል ብዬ አስባለሁ። አንደኛውና የመጀመሪያው በአክራሪነት ላይ የተሟላ ግንዛቤ አለመያዝ ሊሆን ይችላል፡፡ አሁንም ከሃይማኖት አጥባቂነት ጋር አያይዘው እያዩ፣ ሃይማኖትን ባጠበቁት ላይ እየመሠላቸው፣ በቅንነት “መንግስት ለምን በእዚህ መልኩ ይሄዳል” የሚሉት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ሁለተኛው ክፍል ግን ሆን ብሎ እና አውቆ አሁንም የተሰራውን እና ያጀበውን ስራ በማድበስበስ እንዲታለፍ ፈልጎ ሊሆን ይችላል፡፡ እነዚህ ዋና አላማቸው ጉዳዩ ተሸፋፍኖ እንዲታለፍ የሚሹ ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ከህገመንግስታዊ ስርዓታችን ጋር የማይታረቅ ቅራኔ ያላቸው ናቸው፡፡
መንግስት ጉዳዩን በጥንቃቄ አልያዘም፤ ወደ አንድ ወገን ያደላ አቋም አለው ይባላል፡፡ በዚህ ላይ የመንግስት ምላሽ ምንድነው?
በጥንቃቄ መያዝ አለበት የሚሉ ወገኖች አገላለፃቸው ጥሩ ሊሆን ይችላል፡፡ እኛም አክራሪነትና ፅንፈኝነት በጥንቃቄ ነው መያዝ ያለበት ብለን፣ ላለፉት ሁለት አመታት ከሃምሌ 2003 ጀምሮ በሰፊው ህገ መንግስታችንን ለማስተማር፣ የሃይማኖት ተቋማትን በክርስትናውም በእስልምናውም ከራሳቸው ቅዱሳን መፃህፍት መነሻ አድርገው፣ ሃይማኖቶቹ ስለምን እንደሚሰብኩ ለማስተማር ሰፊ እንቅስቃሴ ተደርጓል፡፡ በጥንቃቄ መያዝ አለበት ሲባል እንግዲህ ይሄ ነው፡፡ ሌላው የማይመለከታቸው ሌሎች ወገኖች በዚህ ጉዳዩ ውስጥ እንዳይገቡ ማድረግ ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ በጥንቃቄ መያዝ አለበት ሲባል፣ በምንም አይነት መንገድ ከዚህ ተግባር የማይመለሱ መንግስታዊ ሃይማኖት ለመመስረት አቅደው የሚንቀሳቀሱትን ለይቶ ማስቀመጥ ነው፡፡ በዚህ ላይ ከህዝባችን ጋር ሆነን እኛም ሰዎች በአዕምሯቸው ላይ ባሰቡት ሳይሆን በተጨባጭ የሚገኝ ማስረጃን ይዘን ነው የምንቀሳቀሰው፡፡ ሰዎች እንደቀድሞ ስርዓት ስለተጠረጠሩ ብቻ አይፈረድባቸውም። ይህ አይነቱ ስርአት ዛሬ የለም፡፡ ሠዎች ፍትህን ከትክክለኛው የፍትህ አደባባይ ማግኘት ይችላሉ፡፡ ስለዚህ በጥንቃቄ መያዝ ሲባል አንዱ ማስተማርና ግንዛቤ ማስጨበጥ ነው፡፡ ይህ እንግዲህ ላለፉት ሁለት አመታትም ይሁን አሁን የተኬደበትና እየተኬደበት ያለ ነው፡፡ የህግ የበላይነትን የማስከበር ስራ ሲከናወን ግን መንግስታዊ ስርአት በስርአት አልበኞች እንዲጣስ እየተፈቀደ በሄደ ቁጥር፣ ስርአት አልበኝነት አንደኛው አንደኛውን እየወለደ የሃገራችንን ሠላምና መረጋጋት አደጋ ውስጥ የሚከትበት ሁኔታ ይፈጠራል፡፡ ስለዚህ የሆነ ቦታ ላይ የህግ የበላይነትን የማረጋገጥ ስራ ሲሠራ ጥንቃቄ የጐደለው ነው ተብሎ ሊፈረጅ አይችልም፡፡
መንግስት በጥንቃቄ ጉዳዩን አልያዘውም ከሚያስብሉት አንዱ ወሃቢያን በግልፅ እንደሚቃወም መግለፁ ነው፡፡ በእርግጥስ ይህ ውሣኔ ወገንተኛ አያስብለውም?
የመንግስት ፍረጃ መስፈርቱ አንድ ነው። ህገ መንግስታዊ ስርአትን ተቀብሎ የሚሄድ ነው አይደለም ነው፡፡ ወሃቢያ ነው፣ ሠለፊያ ነው የሚለው አገላለፅ ምናልባት በዚህ ውስጥ ተደራጅተናል የሚሉ ሠዎች በአዕምሯቸው ውስጥ ስለያዙ አይደለም፡፡ በተጨባጭ ከላይ ያስቀመጥነውን ነጥብ ሠዎች ሲጥሡ፣ የዚያ ሃይማኖት ወይም (ሴክት) አባላት ስለሆኑ ሣይሆን ህገ መንግስትን እየጣሱ ስለተገኙ ሊጠየቁ ይገባል፡፡ ይህ መንግስት አንዱን ሴክት ደግፎ ሌላውን ተቃውሟል የሚያሠኝ ነገር ሊያመጣ አይችልም፡፡ መንግስት ሃይማኖቱን ወይም ሴክቱን አይደለም የሚቃወመው፤ ድርጊቱን ነው፡፡ ድርጊቱ ህገ መንግስቱን የሚቃረን ሆኖ እስካልተገኘ ድረስ መንግስት አይመለከተውም፡፡ ለምሣሌ ሠዎች “ወሃቢያ ነኝ” “ሠለፊያ ነኝ” ብለው ቢያምኑ ለምንድን ነው ወሃቢያ የሆናችሁት የሚል ክርክር አናነሣም፡፡ ሠዎች የፈለጉትን የማመን መብታቸው የተረጋገጠ ነው” ለእርምጃዎቻችን መነሻ የምናደርገው ፀረ-ህገ መንግስት የሆነን አክራሪነት ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ለሁሉም ሃይማኖቶች ሲባል ነው፡፡ በእነዚህ ሴክቶች ለሚያምኑት ጭምር፡፡
ማንኛውም ዜጋ ህገ መንግስቱን ማክበርና ማስከበር ይጠበቅበታል፡፡ ይህን ህገ መንግስት አለማክበርን አንዳንዴ የደረቅ ውይይት አካል ያደርጉታል፡፡ ህገ መንግስት ባይከበር እኮ ሁላችንም በሠላም መኖር አንችልም፡፡ የእለቱ ጐበዝ በመጣ ቁጥር ሊያስተዳድረን ይሞክራል ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የወሃቢያን አስተምሮ መንግስት ይቃወማል ለሚለው የምንቃወመውን ክፍል እንቃወማለን፤ የማንቃወመውን ክፍል ግን አንቃወምም፡፡ በወሃቢያ ውስጥ ሆኖ ህገ መንግስቱን ለመናድ የሚሄድ አካል ካለ፣ ወሃቢያ በመሆኑ ብቻ ሣይሆን እያራመደ ያለውን አስተሣሠብ እንቃወማለን፡፡ ያ ፀረ-ህገ መንግስት ነው፡፡ ስለዚህ ተቋሞቹ የፈለገ ስም ቢኖራቸው እኛ ጉዳያችን አይደለም፡፡ ተቋማቱ ውስጥ ሆነው ፀረ-ህገ መንግስት ተግባር የሚፈፅሙ ካሉ፣ መንግስት ህገ-መንግስታዊ ስርአቱን የማስጠበቁን ሃላፊነት እንዲወጣ ይገደዳል፡፡ ህዝቡ እኮ መንግስት አድርጐ ሲመርጠው፣ ህግና ስርአትን ያስከብርልና ብሎ ነው፡፡ ይህ ጉዳይ በእስልምና ውስጥ ብቻ ያለ ተደርጐ መወሠድ የለበትም፡፡ በክርስትና ውስጥም ተመሣሣይ ነገሮች ይካሄዳሉ፡፡

ሌላውን እምነት “እምነት አይደለም” ብሎ የመፈረጅ፣ “ከኔ ጋር እኩል የሆነ ሃይማኖት መኖር የለበትም” የሚሉ አመለካከት ያላቸው አሉ፡፡ “መንግስታዊ ሃይማኖት ካልሆንን፣ ሃይማኖታችን ተዋርዷል፤ ክብርና ሞገሡ ቀንሷል” የሚሉ በክርስትና ሃይማኖት ሽፋንም አለ፡፡ ፍረጃው ተመሣሣይ ነው፡፡ በአንዳንድ የክርስትና ማህበራት ጥላ ስር ያሉ ግለሠቦች ተመሣሣይ አላማና ፍላጐት አላቸው፡፡ ይህን ፍላጐት ለማሣካትም ግንባር ሲፈጥሩም ይስተዋላል፡፡ አንደኛው እስላማዊ መንግስት ለማቋቋም ሲፈልግ፣ አንደኛው ክርስቲያናዊ መንግስት አቋቁማለሁ ነው የሚለው፤ ግን ግንባር ፈጥረው ለመንቀሣቀስ ሲሞክሩ ይስተዋላል፡፡ ይህ እንግዲህ ለሠሚው ግራ ነው። እንዴት አድርጐ ነው የጋራ አላማ ሊኖራቸው የሚችለው፡፡ የጠላቴ ጠላት ጠላቴ ነው በሚል አይነት ፍረጃ የሚሄዱበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ስለዚህ የመንግስት አቋም ሃይማኖቶቹ ምንድናቸው ሣይሆን፣ በነዚህ ተጠልለው ከህገ መንግስቱ የተቃረነ ድርጊት ይፈፅማሉ አይፈፅሙም የሚለው ላይ ትኩረት ማድረግ ነው፡፡ በሞት የተለዩን የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ፤ በተወካዮች ምክር ቤት በግልፅ ተናግረዋል፡፡ እኛ እያልን ያለነው እንዲከበርላቸው የሚሹትን መብት ለሌላውም እንዳይነፍጉ ነው፡፡ እነሡ ግን እያሉ ያሉት ከዚህ መርህ የተቃረነ ነው፡፡ እስቲ አሁን በኛ ሃገር የትኛው መብት ነው የተከለከለው? መፀለይ ነው? የሃይማኖት ተቋም መገንባት ነው? ሃይማኖት ማስፋፋት ነው? የፈለከው ቦታ ተንቀሣቅሠህ አጀንዳህን ማሣካት ነው? የትምህርት ተቋማት እየገነባህ የሃይማኖት ትምህርት ህፃናትና ወጣቶችን ማስተማር ነው? የትኛው ነው የተከለከለው ተብሎ ሲጠየቅ መልስ የለውም፡፡
አንዳንድ ተቃዋሚዎች ከሃይማኖት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን ማንሳታቸው “በእሣት መጫወት” ነው ተብሏል፡፡ መንግስትስ በግልጽ አቋሙን ለይቶ በማስቀመጥ እንዲህ አይነት እንቅስቃሴዎችን ማድረጉ ተገቢ ነው?
አንዱ ህገመንግስታችን ላይ በግልጽ የተቀመጠው፣ ሃይማኖትና መንግስት የተለያዩ ናቸው የሚለው መርህ ነው፡፡ በህገመንግስቱ አንቀጽ 11 ላይ ይህ በማያወላዳ መንገድ የተቀመጠ ነው፡፡ መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ፣ ሃይማኖትም በመንግስት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም የሚል ነው፡፡ እነዚህ ግለሰቦችና ቡድኖች ከሚያነሷቸው ነጥቦች መካከል አንደኛው፣ “መንግስት በሃይማኖት ላይ ጣልቃ ገብቷል፤ እጁን ያውጣ” የሚል መፈክር ነው፡፡ ሁለተኛው፣ “የታሰሩ ይፈቱ” የሚል ነው፡፡ እንግዲህ ፓርቲዎች መንግስት ለመሆን ነው የሚወዳደሩት፡፡ መንግስት ሲሆኑ የመጀመሪያው ተልዕኮ፣ ህገመንግስትን ማክበርና ማስከበር ነው፡፡ ይህ ማለት ለአንድ ሀገር ህልውና በጣም አስፈላጊና ወሳኝ ነው በሚባለው በህገመንግስት ማዕቀፍ ውስጥ የሚታይ የህግ የበላይነት ነው፡፡ ተቃዋሚዎች እያደረጉ ያሉት ለነዚህ ሃይማኖቶች ተቆርቋሪ በመምሠል፣ በሃይማኖቶቹ ተሸፍነን የፖለቲካ ፍላጐታችንን እናሣካለን የሚል ነው፡፡ ትልቅ ስህተት እየሠሩ ነው፡፡ መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባቱ ቢረጋገጥ፣ ይህን የሚያርመው ራሱ መንግስታዊ ስርአቱ ነው። ገዢው ፓርቲ ለምሣሌ እከሌ ጣልቃ ገብቷል ብሎ ሲያስብ፣ የሌላ ሠው አስታዋሽ ሣይፈልግ ራሱን በራሱ ነው የሚያርመው፡፡ መንግስት ህገ መንግስቱ ተጥሷል ብሎ የሚወስዳቸው እርምጃዎች ከሃይማኖት ጋር ግንኙነት የላቸውም፡፡ ምክንያቱም ያ ፀረ-ህገ መንግስታዊ የሆነ እንቅስቃሴ ሃይማኖታዊ አይደለም፡፡ ስለዚህ መንግስት ጣልቃ ገብቷል የሚለው አገላለፅ አንድም ተራ የሆነ ተወዳጅነትና ተቀባይነት እናተርፋለን ተብሎ የሚቀርብ ዜና ነው፤ በሌላ በኩል የህግ መሠረት የሌለውና እነዚህ ፓርቲዎት መድረሻቸውም መነሻቸውም ህገ መንግስታዊ ስርአትን የማክበርና የማስከበር ሣይሆን ሌላ ፍላጐት እንዳላቸው የሚያሣይ ነው፡፡
እዚህ ላይ የሚታየው አንዱ “የታሠሩ ይፈቱ” የሚለው መፈክር ነው፡፡ በመግለጫችንም በተለያዩ አጋጣሚዎችም አንስተነዋል “የታሠሩ ይፈቱ” የሚል ፍላጎት በግለሠቦቹ አዕምሮ ውስጥ ሊኖር ይችላል፤ ነገር ግን አባባሉ በቀጥታ ከህግ የበላይነት ጋር የሚጋጭ ነው፡፡ “የሠማያዊ ፓርቲን” አጅበውና አሣጅበው ይህን ጥያቄ ለተወሠኑ አካላት አቅርበው ሲሄዱ፣ በቀጥታ እንዳሉት በዚህች ሃገር ውስጥ የዳኝነት ስርአት የሚባል ነገር በግለሠቦች ቅስቀሣ ይደፈቃል ማለት ነው፡፡ ለዚህም ሊያደራጅ የሚችል በሙሉ “ይፈታ” እያለ የሚያስፈታ ከሆነ፣ የህግ የበላይነት በአጃቢው ፅንፍ የሚወድቅበት ሁኔታን ነው እያሣዩ ያሉት፡፡ ስለዚህ ፓርቲዎች ህገመንግስታዊ ስርአቱንም ህጋዊ ስርአቱን እንዲሁም የዳኝነት ስርአቱንም ጭምር የሚጥስ ስራ ላይ ነው የገቡት፡፡ እነሱ ፓርቲ እንዲሆኑ በር የከፈተላቸውን ህገመንግስት ጭምር ነው እየደፈቁ ያሉት፤ በዚህ አይነት መንገድ ፓርቲ ሊሆኑ አይችሉም ማለት ነው፡፡ በዚህ መንገድ ለመሄድ የሚያስቡት ሙከራም እግሩ በጣም አጭር ነው፡፡ በራሳቸው ህልውናም ጭምር ፈተና የሚደቅንም ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም ከሃይማኖቶቹ ገለጥ አድርገህ ስታያቸው ባዶ ናቸው ማለት ነው፡፡ እነዚህ ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ ከአክራሪና ከጽንፈኛ ሃይሎች ጋር አብረው የሚሰለፉ ከሆነ የመጀመሪያው ጉዳይ የሚሆነው አክራሪነትንና አሸባሪነትን እየደገፉ ነው ማለት ነው፡፡ ሰውን በእምነቱ ምክንያት በጠራራ ፀሐይ ከሚገድሉ ጋር ፓርቲው የሚያብር ከሆነ፣ በአለማቀፍ ህግም በሃገራችን ህጐችም፣ በፀረ ሽብር ህጉም ጭምር እነዚህ ሰዎች የማይጠየቁበት ምክንያት የለም፡፡ አሸባሪነትን “ጐሽ፤ አይዞህ በርታ” ማለት በፀረ ሽብር ህጉ የሚያስጠይቅ ነው፡፡
ተቃዋሚዎች “የፀረ-ሽብር ህጉ አፋኝ ነው” በሚል ተደጋጋሚ ቅሬታ ያቀርባሉ፡፡ አንዳንዶችም ለማሰረዝ እየተንቀሳቀሱ ነው፡፡ መንግስት በህጉ ላይ ለምን ከተቃዋሚዎች የሚቀርቡለትን ማስረጃዎች ተመልክቶ በጉዳዩ ላይ ከነዚህ አካላት ጋር አይወያይም?
በፀረ-ሽብር ህጉ ላይ በአመለካከት ምክንያት የሚጠየቅ ሰው የለም፡፡ የአመለካከት ነፃነት በህገመንግስታችን ዋስትና የተሰጠው ተፈጥሯዊ እውነት ነው ተብሎ የሚወሰድ ነው፡፡ በአመለካከት ምክንያት ተጠያቂ ሆነናል የሚሉ ሰዎች አቀራረብ አታላይነት ነው፡፡ በየመጽሔቱ፣ በየጋዜጣው ስንት ነገር ይባላል እኮ፤ ግን እንደዚህ አይነት አመለካከት ይዘሃል ተብሎ የሚጠየቅ ሰው የለም። ሆኖም በየትኛውም መንገድ ህዝብን ወደ ሽብርና አለመረጋጋት እንዲሁም እምቢተኝነት መምራት የተከለከለ ነው፡፡

ይሄ ሃገራችንም ከተቀበለቻቸው አለማቀፍ ህጐች ጋርም ተያይዞ የሚታይ ነው፡፡ ፀረ ሽብር ህጉ ሰውን ተጠያቂ የሚያደርገው፣ በተግባር በዚህ ውስጥ ግለሰቦች ተሳትፈው ሲገኙ ነው፡፡ በሀገራችን በየቀኑ ቦምብ ስለማይፈነዳና ሠላማዊ ዜጐች ሰለባ ስለማይሆኑ፣ ይህን ሃሳብ የሚያቀርቡ ግለሰቦች ጭምር በሰላም ውለው ስለሚገቡ፣ ምንም ስራ ሳይሰራ እንዲሁ መሽቶ እንደሚነጋ ስለሚያስቡ ነው፡፡ ይህን ሰላምና ደህንነት ለማስከበር ብዙ የሀገራችን ዜጐች ሌት ተቀን እንደሚሰሩ አይገነዘቡም ማለት ነው፡፡ የሽብርን አደጋ ቀድሞ የመከላከል ስራ በመሠራቱ፣ ሠላም ማግኘታቸውን አይረዱም ማለት ነው፡፡
ስለዚህ የፀረ ሽብር ህጉ፣ በተለየ መንገድ ሰዎችን ለማጥቃት የተዘጋጀ ነው የሚሉ ሰዎች መጀመሪያውኑ በሽብር ላይ ለመሳተፍ ካላቸው ፍላጐት የሚመነጭ ካልሆነ በስተቀር፣ የሚጠብቃቸው ህግ እንጂ ሽብርተኛ ሆናችኋል ብሎ የሚያስራቸው ህግ አይደለም፡፡ ይህ ደግሞ የኢትዮጵያ ህዝብ ፍላጐት አይደለም፡፡ ይህ ህግ እኮ ደጋግመን እንደምንለው አሉ ከተባሉ አለማቀፍ ህጐች የተቀዳ ነው፡፡ በሌላ በኩል የአንድ ሚሊዮን ሰዎችን ፊርማ እናሰባስባለን ብለው የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦች በአደባባይ ከአክራሪነትና ጽንፈኛነት መፈክሮች ጀምሮ፣ በአሸባሪዎች ይፈፀሙ የነበሩ ድርጊቶችን ሳያወግዙ ግን በሌላ በኩል የአክራሪነትና ጽንፈኝነት ተዋንያኖች ሆነው ታይተዋል፡፡ ስለዚህ እነሱ በዚህ አይነት ሲንቀሳቀሱ ህዝባችን ይዳኛቸዋል ብለን እናስባለን፡፡ ዙሪያችን በሙሉ ምን እንደሆነ እናውቃለን ግን ከውጭ ፖሊሲያችን ተነስተን፣ ጨለማ ነው ብለን አናስቀምጥም፤ ብርሃን ነው ብለን ነው የምናስቀምጠው፡፡

ግን ጥንቃቄ የሚሻ ብርሃን ነው ያለው፡፡ ሶማሊያ ያለውን እናውቃለን፣ በኤርትራ ገዢ ፓርቲ በኩል ያለውን ፍላጐት እናውቃለን፤ ሌሎችም በተለያዩ ምክንያቶች የጀመርናቸውን ልማቶች ለማደናቀፍ ምን አይነት ስልቶችን ሊጠቀሙ እንደሚችሉ መገመት ይቻላል። እነዚህን እኩይ ስልቶችን ለማክሸፍ የውስጥ ተጋላጭነትን ማስወገድ ያስፈልጋል፡፡ ይህን ለማድረግ ድህነትን ማጥፋት ዋናው ተግባር ነው፡፡ በሚገባ የሚበላ የሚጠጣ ሰው በትንሹ አይደለልም። ኋላ ቀርነታችን ለእንደዚህ አይነት ጉዳይ ተጋላጭ ያደርገናል፡፡
የራሳቸውን ሃገር መልሰው የሚወጉ ባንዳዎችም አይጠፉም፡፡ መንግስት ለምንድን ነው ማሳያዎችን አምጡ ብሎ ጉዳዩን የማያጤነው ለሚለው፣ በእርግጥም የተወሰኑ ብዥታዎች ላላቸው ሰዎች እንደዚህ አይነት አገላለጽ ሊጠቅም ይችላል። ለህዝባችን በዚህ ዙሪያ ላይ ግልጽ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ እነዚህ አካላት ግን ኑ ተብለው ብታስረዳቸውም የሚቀበሉ አይደሉም፡፡ መነሻቸውን ስለሚያውቁ የሚያመቻቹት የገቡባትን ቀዳዳ መሸፈኛ የሚሆናቸውን ብቻ ነው፡፡ በዚህም ውይይት እየተደረገ ቢዋል ቢታደር አሳምነው ወይም አምነው የሚሄዱ አይደለም፤ ስለዚህ ጉዳዩን በተለያዩ ብዥታዎች ተሸፍኖ እንዳይሄድ በውይይት ግልጽ መደረግ አለበት የሚለው ሊያስኬድ የሚችል ቢሆንም፣ እነዚህ ሃይሎች ለዚህ ያላቸው ፍላጐት አነስተኛ ነው፡፡
መንግስት፤ ለምን አስቀድሞ አክራሪዎች የሚላቸውን ወገኖች ጥያቄ በአደባባይም ይሁን በሌላ መንገድ ነፃ ሆነው እንዲያቀርቡ እድል አልሰጣቸውም? ለምንስ አይሰጣቸውም?
እንደዚህ አይነት ሃሳብ የሚያቀርቡ ወገኖች ካሉ መረጃ ስለሌላቸው ነው፡፡ አስቀድሜ ሳነሳው እንደነበረው፣ አክራሪዎቹና ጽንፈኞቹ ባለፉት 30 እና 40 አመታት የአክራሪነትና ጽንፈኝነት ስራ ሲያስተምሩ ቆይተዋል፡፡ አክራሪነትና ጽንፈኝነትን ሲያስተምሩ በነበረበት ወቅት “ለምን ይህን ታደርጋላችሁ” ብሎ ያስቆማቸው ሰው አልነበረም። አሁን ለምንድን ነው ጉዳዩ ገንፍሎ የወጣው ሲባል፣ የኢትዮጵያ እስልምና ምክር ቤት ይህን አክራሪነትና ጽንፈኝነት ማጋለጥ የሚችልበትን ትምህርት ማስተማር መጀመሩ ነው፡፡ ይህን ትምህርት “መንግስት ከመጅልሱ ጋር ሆኖ መበቲ ሃይማኖትን አምጥቶብናል” በሚል በከፍተኛ ደረጃ አብጠልጥለውት ነበር፡፡ አንዳንድ ቦታዎች ላይም “አህባሽ የሚባል ሃይማኖት መንግስት አምጥቷል” በሚል ሰፊ ቅስቀሳ ተደርጓል፡፡ ህገመንግስታችን ማንም የፈለገውን ማስተማር እንደሚችል በግልጽ ያስቀምጣል፡፡ አክራሪው ሃይልም ባለፉት 30 እና 40 አመታት የፈለገውን ትምህርት ሲያስተምር ቆይቷል። ለዚያ የሚሆኑትን ተቋማት ሲገነባ ቆይቷል፡፡ ሃምሌ 2003 ዓ.ም አካባቢ መጅሊሱ ትክክለኛው የሃገራችን የእስልምና ሃይማኖት አስተምህሮ ምንድን ነው በሚል ማስተማር ሲጀምር፣ የአክራሪውና የጽንፈኛው ቡድን ማንነት መጋለጥ ጀመረ፡፡ ይህ መጋለጥ ሲጀምር እጅግ በሰፊ መንገድ መጅሊሱን መቃወም ጀምረዋል፡፡ መጅሊሱ የሚወክለን አይደለም፤ በበር ሳይሆን በመስኮት ነው የመጣው በሚል ማለት ነው፡፡ በዚህ እንግዲህ አክራሪነቱ በግላጭ እየመጣ ሄደ፡፡
የመጅሊሱ አስተምህሮ በዚህ ከቀጠለ የኛን ህልውና ጥያቄ ውስጥ ያስገባዋል፤ ስለዚህ በምንችለው ሁኔታ ይህ እንዳይሆን መፍጨርጨር አለብን የሚል ሃሳብ አመጡ፡፡ ይህን ሲያነሱ የተለያዩ የራሳቸውን አደረጃጀት እየፈጠሩ በተለይ አርብ ጁምአ በመጣ ቁጥር፣ እጅግ በጣም ሰፊ የሚባል ህዝብን እያንቀሳቀሱ ለመሄድ ይሞክሩ ነበር፡፡ ይህን ሲያደርጉ በጣም ብዙ መድረኮች ተከፍተው “ጥያቄያችሁ ምንድነው” ተብለው ተጠይቀዋል። ስለዚህ መንግስት በተለይም አስተባባሪዎችና መፍትሔ አፈላላጊዎች ነን የሚሉ ቡድኖችን ከሦስት ጊዜ በላይ አግኝተን አነጋግረናቸዋል፡፡ የተለያዩ መዋቅሮቻችንም በየራሳቸው አግኝተው አነጋግረዋቸዋል፡፡ በራሳችን መዋቅር ግን መፍትሔ አፈላላጊ የተባሉትን ቡድን ለማነጋገር ተሞክሯል፡፡ “ከአሸባሪ ድርጅቶች ጋር ትሠራላችሁ፤ ከኦነግ ጋር ከአልሸባብ፣ ከግንቦት 7 ጋር ትሠራላችሁ፤ የናንተን ድምጽ እነዚያ ያስተጋባሉ፤ የእነሱን ድምጽ እናንተ ታስተጋባላችሁ፤ ይህ ሃይማኖት ጥያቄ አይደለም” ብለናቸዋል፡፡ መጨረሻ አካባቢ እንደውም ከአልሸባብና ከአልቃኢዳ ህዋስ ጋር የመተሳሰር ነገርም ነበር፡፡

ያም ሆነ ይህ ሃይማኖታዊ ጉዳይ የምትሏቸውን አምጧቸው፤ እኛ እንደመንግስት የሚያገባን ነገር ካለ እንወያይባቸው ብለን ነበር። አንደኛው ያነሱት የስልጠና ጉዳይ ነው፡፡ አህባሽ የሚባለው ስልጠና ላይ የተነሳ ጥያቄ ነው፡፡ እኛ የትኛውም አስተምህሮ ይቅረብ፤ ህገመንግስቱንና ህገመንግስታዊ ስርአቱን አደጋ ላይ የሚጥል እስካልሆነ ድረስ ግድየለንም፣ ስለዚህ ማን ምን አስተማረ የሚለው ህገመንግስትን የሚጥስ ነው የማይጥስ ነው በሚለው መስፈርት ነው፣ የሚጥስ ትምህርት ስታስተምሩ እንኳ አቁሙ አልተባላችሁም ብለናቸው፡፡ በዚህ ጉዳይ በግልጽ ተወያይተናል፡፡
ሁለተኛው መጅሊሱ የሚወክለን ተቋም አይደለም የሚለው ነው፡፡ መጅሊሱ የማይወክላችሁ ከሆነ የሚወክላችሁን ተቋም ማቋቋም የእናንተ መብት ነው፡፡ በዚያ ጉዳይ ላይ የምናግዛችሁ ካለ እናግዛችሁ፡፡ ለምሣሌ አዳራሾችን በመፍቀድ ፀጥታና ሠላም በማስጠበቅ ልናግዛችሁ እንችላለን፡፡ ይህን ስታደርጉ ደግሞ ብይን የሚሰጠው የኢላማ ምክር ቤት በሚሠጠው ውሣኔ መሠረት መሄድ አለብን በሚል ተነጋገርን፡፡ ምርጫው ተካሄደ፡፡ ከ8 ሚሊዮን በላይ መራጭ የተሣተፈበት ነበር፡፡ ነገር ግን እነዚህ ሃይሎች ይህንንም ምርጫ የማብጠልጠል ነገር ውስጥ ተዘፍቀው ተገኙ፡፡ እንግዲህ የዚህ ሁሉ ምክንያት ሠዎች መነሻቸውን ስለሚያውቁ፣ የሌላው ማብራሪያ ስለማያሣምናቸው ነው፡፡ መሃል ላይ ተግባብተናል ብለው በተግባቡት መንገድ ለመሄድ አይፈልጉም፡፡ ሌላው ከአውሊያ ትምህርት ቤት ጋር ተያይዞ የተነሣው ነው፡፡ አወሊያ ት/ት/ኮሌጅ በውጭ የእስልምና እርዳታ ተቋማት ድጋፍ የተቋቋመ ነው፡፡ መነሻው ላይ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ለበጐ ጉዳይ አቋቋሙት ነው የሚባለው። ኋላ ግን አንዳንድ ነገር ማስኬድ ሲቸግራቸው ይመስለኛል እነዚህ አለማቀፍ ተቋማት ይገባሉ። ይገቡና አጠቃላይ ከሚመለምሏቸው መምህራን ጀምሮ፣ በአረቢኛ ቋንቋ ሽፋን የሚያስተምሩት ትምህርት የአክራሪነት እና ፅንፈኛነት ትምህርት ነው፡፡ ይህንንም ለማስተካከል ተሞከረ፤ እንደዚህ እያለ ይቀጥልና መጨረሻ ላይ የተነሣው “የታሠሩ ይፈቱ” ነው፡፡ “የታሠሩ ይፈቱ” የሚለው ከህግ የበላይነት ጋር የሚፃረር ነው፡፡ እንግዲህ በእነዚህ ጉዳዮች ሁሉ ይመለከታቸዋል ከተባሉት ጋር ሁሉ ውይይት ተደርጓል፡፡ ስለዚህ መንግስት በር ዘግቶ፣ “ከእናንተ ጋር ውይይት አላደርግም” አላለም፡፡ የአክራሪው ቡድን ግን ለምሣሌ የዛሬ አመት እንደ ነገ የአፍሪካ ህብረት ስብሠባ ሊካሄድ ሆኖ እያለ፣ አንድ ሚሊዮን ህዝብ ሠልፍ ጠርተናል ብሎ አዲስ አበባን ለማመስ ተንቀሣቅሠዋል፡፡ እኩለ ለሊት ላይ የአዛን ደውል አስደውለው፣ “አሁን እያንዳንድህ ጐረቤትህን ማጥቃት ያለብህ ጊዜ ነው” የሚል ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡

ይህ ማለት በጣም አደገኛ ሴራ ማለት ነው፡፡ እዚህ አይነት ደረጃም ደርሠው ነበር። ኋላ ላይ ግን እነዚህ ሠዎች ፍላጐታቸው የህዝብ መተላለቅ መሆኑን ህዝብ ሙስሊሙ እየተረዳ ሲመጣ፣ ባዶአቸውን ትቷቸው ሄዷል፡፡ አሁን የእነሡ ደጋፊዎችና አጫፋሪዎች ያሉት ኢትዮጵያ ውስጥ ሣይሆን ከኢትዮጵያ ውጪ ናቸው። በማህበራዊ ሚዲያዎች (ፓልቶክ፣ ፌስቡክ) ብዙ ሲያወሩና ሲያስወሩ ይሠማል፡፡ አሁን ላይ እንደውም ኢትዮጵያ ውስጥ የአርብ ፀሎት የለም የሚል እያስወሩ ነው፣ ሴቶች ሃይማኖቱ የሚያዘውን አለባበስ ተከልክለዋል፣ የስግደት አካሄድ ተቀይሯል የሚሉ የፈጠራ ወሬዎችንም እያስወሩ ነው፡፡ የእነዚህ ሠዎች አላማ እንግዲህ በሃገራችን የታየውን ብርሃን መልሶ የማጨለም ነው፡፡ እንግዲህ አስቀድሜ እንዳልኩት፤ በፌደራል ጉዳዮች ለውይይት የተዘጋ በር የለም፡፡ ሁለት አመት ሙሉ የውይይት ጊዜ ነበር፤ አሁንም መንግስት በሩ ክፍት ነው፡፡ ነገር ግን እነዚህ ሠዎች የማይታረቅ ቅራኔ ነው ያላቸው፡፡

ባለፈው ደሴ ላይ ሠው ተገድሏል፡፡ ባሌ ውስጥም የአንደኛው የታወቁ አሊም መቃብር ቆፍረው አስክሬናቸውን ሲያቃጥሉ ነበር፡፡ በነገራችን ላይ ከነዚህ ግለሠቦች አንዳንዶቹ በዚህ ሽፋን ምንም ሣይኖራቸው በማግስቱ ሚሊየነር የሆኑ ናቸው። ስለዚህ ይህ አጀንዳ ተዘጋ ማለት፣ ለአንዳንዶቹ የመኖር ህልውናቸው አከተመ ማለት ነው፡፡
እርሶም እንዳሉት በአንድ በኩል በማህበራዊ ድረገፆች የሚካሄዱ ቅስቀሣዎች አሉ፡፡ በሌላ በኩል ከተቃዋሚዎች ጥያቄ ጋር ተያይዞ የሚነሣ አለ፡፡ በአንድ ወገን ደግሞ የመንግስት አቋም አለ፡፡ እነዚህ ሶስት አካላት የያዙት የተካረረ የሚመስል አቋም የዚህችን ሃገር መፃኢ እድል አስጊ አያደርገውም? መጨረሻውስ ምንድን ነው የሚሆነው?
የሚሆነው የሚመስለኝ ውሸት እግሩ አጭር ነው፡፡ የአንድ ሠሞን ግርግር አካል ሊሆኑ ይችላሉ። ከዚያ ባለፈ ግን ለህዝባችን ህይወቱን የሚቀይር ነገር እንደሌላቸው በሂደት እየተጋለጡ ነው፡፡ ህዝባችን ከማህበራዊ ድረ ገፅም ከተቃዋሚ ፓርቲም የሚፈልገው፣ “እንዴት ሆኖ ከድህነት እንወጣለን” የሚለውን የሚያሣየውን እንጂ የተመለሡ ጥያቄዎችን ያልተመለሡ አድርገው ከበሮ መምታትን አይደለም፡፡ ለዚህም ተባባሪ አይሆንም፡፡ በመጨረሻ ፈራጅ የሚሆነው ህዝቡ ነው፡፡ ህዝቡ ከበሮ ስለተመታ ይሁንታ አይሰጥም፡፡ ማነው ለልማት ደፋ ቀና እያለ ያለው? ማነው ልማትን ለማደናቀፍ የሚተጋው? የሚለው ሁሉም ሠው እየለየው ሊሄድ ይችላል፡፡ ሁሉንም ተቃዋሚዎች የሚመለከት ባይሆንም፣ የተቃዋሚዎች በዚህ አይነት መሄድ ግን መጨረሻቸው የማያምር ነው፡፡ እነዚህ ሃይሎች መንግስት ለመሆን ፍላጐት የላቸውም ማለት ነው። አንዳንድ ልሂቃን የሚያስቀምጡት ነገር አለ። አንድ ሃይማኖት ሲኖር አምባገነንነት ነው፣ ሁለት ሃይማኖት ሲኖር ጦርነት ነው፣ ብዙ ሃይማኖት ሲኖር ሠላም ነው፤ የኛን ሃገር የሚገልፀው ሶስተኛው ነው። በዚህች ሃገር ውስጥ አንደኛው ካለ አንደኛው እኖራለሁ ብሎ የሚያስብበት ሁኔታ የለም፡፡ ስለዚህ እነዚህ አካላት የሃሣብ ልዩነት ቢኖራቸው እንኳ የህዝባችንን ይሁንታና ፍርድ አክብረው መሄዳቸዉ የሚመከር ነው፡፡ ይህ ካልሆነ ያለፈው ትውልድ ድህነትና ኋላቀርነት እንዳስተላለፈልን ሁሉ ይሄኛው ትውልድ ደግሞ አክራሪነትንና ፅንፈኛነትን ለቀጣዩ ትውልድ ሊያስተላልፈው ነው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ያ እንዳይሆን ሁላችንም በየራሣችን ድርሻ መጪውን ጊዜ ከግምት ያስገባ ስራ መስራት አለብን፡፡
የአውሮፓ ህብረት በቅርቡ የሠጠውን መግለጫ ጨምሮ ከተለየዩ አለማቀፍ ተቋማት እየወጡ ያሉ ሪፖርቶች ኢትዮጵያ ከሃይማኖት ጋር የተያያዘ የመብት ጥሠት ትፈፅማለት የሚሉ ናቸው፡፡ ሚ/ር መስሪያ ቤቱ እነዚህን ሪፖርቶች እንዴት ነው የሚገመግማቸው በሃገራችን ገፅታ ላይስ አሉታዊ አስተዋፅኦ አይኖረውም?
የአውሮፓ ህብረት እንዲህ ያለ መግለጫ መስጠቱን አልሠማሁም ሠጥተው ከሆነ ሃገራችንን የማይገልፅ ነው፡፡ ስለ ሃገራችን ሃይማኖቶች እና እምነቶች ባለፉት 20 አመታት የነበሩ ተጨባጭ እውነታዎች የሚመክሩት ነው፡፡ ሌላ መስካሪ ሣያስፈልገን የኛ ዋነኛ መስካሪ ህዝባችን ነው። ይህ ደግሞ በየእለቱ በሚያከናውነው ተግባሩ የሚገለፅ ነው፡፡ በየአርቡ፣ ቅዳሜ እና እሁድ በየራሱ አምልኮ ላይ በነፃነት የሚሣተፈው ህዝብ ነው የሚመሠክረው፡፡ መናገርና ሆኖ መገኘት የተለያዩ ነገሮች ናቸው፡፡ የራሣቸውን ፍላጐት ለማሣካት ካልሆነ በስተቀር የሃገራችንን ነባራዊ ሁኔታ የሚገልፅ አይደለም፡፡

 

ተነደን ጠንተነ ጋዳኔ መራ ወሮፐ (የወላይትኛ ተረት)
ከኤዞፕ ታሪኮች ውስጥ ጃክዶ ስለሚባል አንድ መጠኑ መካከለኛ የሆነ ቁራ - መሳይ ወፍ የሚከተለው ይገኛል፡፡
ጃክዶ በአውሮፓም በእስያም የሚገኝ ወፍ ነው፡፡ መልኩ የጥቁርና የግራጫ ቀለም ድብልቅ ነው፡፡ የሚያብረቀርቅ ነገር መልቀምና መስረቅ የሚወድ ለፍላፊ የወፍ ዘር ነው፡፡
ጃክዶ እርግቦችን ባየ ጊዜ በጣም አድርጐ ይቀናል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት እርግብ ያገኝና ወዳጁ ሊያደርጋት ይጠጋታል፡፡
ጃክዶ - “እመት እርግብ” ይላታል
እርግቢት - “አቤት” ትላለች
ጃክዶ - “የእናንተ ቤተ - እርግብ (ቤተሰብ) እኮ በጣም የታደለ ነው”
እርግቢት - “እንዴት?”
ጃክዶ - “የሰው ልጅ ስለሚመግባችሁ የትም የትም ምግብ ፍለጋ አትንከራተቱም”
እርግቢት - “ዕውነትክን ነው - በሱስ እግዜር አድሎናል፤ ገላግሎናል”
ጃክዶ - “የሰው ልጅ የቤቱን ጣራ፣ የመስኮትና የበር ደፍ ሳይቀር ለመኖሪያ ቤት ሰጥቷችኋል።
እኛን ተመልከቺ፡፡ የምንኖረው በየቋጥኙ ሽንቁርና በየጭስ ማውጫው ጥላሸት ላይ ነው፡፡”
እርግቢት - “አዎን፡፡ የሰው ልጅ ባለውለታችን ነው”
ጃክዶ - “በዛ ላይ ከሶስት መቶ በላይ ዝርያ ስላላችሁ ጠላት ቢመጣባችሁ ለመከላከል ትችላላችሁ፡፡ ሐዘን ቢደርስባችሁ ትስተዛዘናላችሁ፡፡ ብትፈልጉ ትመሣጠራላችሁ፡፡ ማሕበር ቢያሻችሁ ማሕበር መሥርታችሁ ትተጋገዛላችሁ፡፡ እኛ የጃክዶ ዝርያዎች እንደዛ ዓይነት መረዳዳት አናቅም፡፡ ስለዚህ በጣም ታስቀኑኛላችሁ፡፡
እርግቢት - “ልክ ነህ ብዙዎች የወፍ ዝርያዎች እንደሚቀኑብን ይነግሩናል፡፡ የተፈጥሮ ነገር ስለሆነ ምን ታደርገዋለህ” ትለዋለች፡፡
ጃክዶ በእርግቢቱ በኩል የእርግቦችን አኗኗር ሲያጠና ይቆያል፡፡ ከዚያም አንድ ቀን፤
“ቅርፄንና ቀለሜን እንደነሱ አድርጌ ከነሱ ተቀላቅዬ፤ የእነሱን ጥቅምና ምቾት ማግኘት አለብኝ” ብሎ ያስባል፡፡ ከዚያም መላ አካሉን የነጭ እርግቦች ቀለም ይቀባል፡፡ ድምፁን በተቻለ መጠን በእነሱ ቅላፄ ለመቅረጽ ይለማመዳል፡፡ ሆኖም ብዙ ላለመናገር ይወስናል፡፡
አንድ ቀን በግሪሣ ከሚበርሩት እርግቦች ጋር ይቀላቀልና ይበርራል፡፡ ለብዙ ጊዜ እርግቦችን መስሎ፤ እርግቦችን አክሎ ኖረ፡፡ ሆኖም ከእነሱጋር ብዙ በኖረ ቁጥር ምቾት እየተሰማው፤ እንደጉራም እየተሰማው፤ የባለቤቱ ልጅ የሆነ መሰለው፡፡ ብዙ እርግቦች በተሰበሰቡበት ሸንጐ ላይ ንግግር አደረገ፡፡ ብዙ በተናገረ ቁጥር የድምፁ ቅላፄ ወደ ጃክዶዎች ቅላፄ መምጣት ጀመረ፡፡
እርግቦቹ ተያዩና የነሱ ዝርያ እንዳልሆነ ለዩት፡፡ ወዲያው በአንድ ቅጽበት ሰፈሩበትና እንዳይሞት እንዳይሽር አርገው ተክትከው ተክትከው አባረሩት፡፡
ጃክዶውም አዝኖና ቆሳስሎ ወደዘመዶቹ ሄደ፡፡ ዘመዶቹ ግን ነጭ ቀለሙን ሲያዩ “የእኛ ዝርያ ቤተሰብ አይደለህም ዞር በል ከዚህ” ብለው አባረሩት፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ያ ጃክዶ ቤት አልባ ሆኖ፣ ማረፊያ አጥቶ ይንከራተታል፡፡
* * *
መምሰል ክፉ በሽታ ነው፡፡ ለጥቅምም ሆነ ለአንዳች ግላዊ ዒላማ ብሎ ሌሎችን መስሎ፣ የሌሎችን ማሊያ ለብሶ፣ የሌሎችን ዜማ አጥንቶ፤ እንደሌሎች እሆናለሁ ብሎ ማሰብ፤ “የባዳ ሞኝ ከልጅህ እኩል አርገኝ” አለ፤ እንደሚባለው ነው፡፡ የተቀቡት ቀለም መደብዘዙ፣ ያጠኑት ዜማ መፍዘዙ እና የራስ ማንነት የማታ ማታ በዚህም ቢሉት በዚያ ብቅ ማለቱ አይቀሬ ነው፡፡ በሥነ - አዕምሮ ጠበብት እስስታዊ ባህሪ የሚሉት ነው፡፡ ፖለቲከኞች አድር - ባይነት የሚሉት ነው፡፡
ገጣሚዎች ደሞ፤
“ያካባቢ ቀለም ብትለብስም፣ እስስት የኖረች መስሏት
የማይወላውል ባላንጣ፣ አድብቶ ለቀም አረጋት!
ቀን የተመቸን መስሎን፣ የኛ ካልሆነ መጠጋት
የጅሎች አጉል ብልጠት
ለ”አስብቶ - አራጅ” እጅን መስጠት
የሰው ቀለም ፍለጋ፣ የራስን ቀለም ማጣት!
የዛም የዚህም ሳይሆኑ፣ ምላስ አርዝሞ መቅረት (Extensile Tongue) –
ሀምሌ 19/2005 ዓ.ም (ለረዣዥም ምላሶችና ለልበ እስስቶች)
ረዣዥም ምላሶችና ልበ - እስስቶች የትም አሉ፡፡ በቢሮክራሲ ውስጥ፡፡ በፓርቲ ውስጥ፡፡ በኩባንያ ውስጥ፡፡ በንግድ ውስጥ፡፡ በወጣት ውስጥ፡፡ በአዋቂ ውስጥ፡፡ በሴት ውስጥ፡፡ ነቅተው ካልጠበቋቸው ለግንዱም ለቅርንጫፉም አስጊ የሚሆኑበት ጊዜ ይመጣል፡፡
ከላይ የተጠቀሰው የተረቱ ጃክዶ “በጳጳሱ ዙፋን ላይ በኩራት ይቀመጣል፡፡ ካህኑም፣ አባውም፣ ዲያቁንም ቢኖሩ ግድ የለውም” ይላሉ ፀሐፍት በምፀት፡፡ ለዚህም ነው የዱሮ ፖለቲከኞች “አድርባዮች ያሉበት አብዮት ከመቦርቦር አይድንም” የሚሉት፡፡
ጥንት የሀገራችን መሪ ባለስልጣናቱን ሰብስበው፤
“ከዚህ ከዚህ ክፍለሀገር በሀገር ውስጥ ገቢ ያልተሰበሰበ ይሄን ያህል ሚሊዮን አለ ተብሏል። እሺ የክፍለ ሀገሩ አስተዳዳሪ ምን ትላለህ” ብለው ጠየቁት አሉ፡፡ አስተዳዳሪውም ወታደር ነበረና ተነስቶ ግጥም አድርጐ ሰላምታ ከሰጠ በኋላ፤
“አለ ጌታዬ! አመጣለሁ!” አለ ይባላል፡፡
ቢሮክራሲና ካፒታሊዝም ቀለበት ካሰሩ ሰነባብተዋል፡፡ ሥልጣንና ንግድ ከተጋቡ ውለው አድረዋል፡፡ አሁን ጥያቄው Who guard the guards? ጠባቂዎቹንስ እነማን ይጠብቋቸዋል? የሚለው ነው፡፡ አንድ የዘመኑ ማስታወቂያ አከል መልዕክት፡- “ማፍረስ ቀላል ባይሆንም፤ መገንባት የበለጠ ከባድ ነው!” (የደርግ መፈክር)
ዛሬ በንግድ የሚተዳደሩ ቢሮክራቶች፣ የድርጅት መሪዎች እየበዙ ነው፡፡ የፖለቲካ መሪዎች ብዛትማ አይጣል! አስተዋይ ዐይን ተከፍቶ ቢያያቸው ይበጃል፡፡ “እንደኔ አጠባለሁ ብለሽ ጥጃሽን አትግደይ!” የሚለው የወላይትኛ ተረት ጡታቸው ላይ ማነጣጠር አለበት፡፡

Published in ርዕሰ አንቀፅ

በማሽኖች ግዢና ኪራይ ከፍተኛ ሙስና ፈጽመዋል ተብለው ከሚፈለጉ 25 የኦሮሚያ ውሃ ስራዎች ኮንስትራክሽን ባለስልጣናት መካከል 13ቱ የተያዙ ሲሆን፤ የድርጅቱ ዋና ስራ አስኪያጅና ምክትላቸውን ጨምሮ ዋና ዋና ሃላፊዎች እስካሁን አልተያዙም፡፡ ዘንድሮ አንድ ሺህ የሚጠጉ ጥቆማዎች እንደቀረቡ የኦሮሚያ ፀረ ሙስና ኮሚሽን የኮሙኒኬሽንና የትምህርት ክፍል ሃላፊ አቶ ጠይብ አባፎጊ፤ ጥቅሞች መነሻነት ከ250 በላይ የምርመራ መዝገቦች ተከፍተዋል፤ የውሃ ስራዎች ኮንስትራክሽን ድርጅት ሃላፊዎች ላይ የተከፈተው የምርመራ መዝገቡም ከእነዚህ አንዱ ነው ብለዋል፡፡

የድርጅቱ ቦርድ ዋና ፀሐፊ፣ ዋና ስራአስኪያጅና ምክትላቸው፣ እንዲሁም የፋይናንስና የማሽነሪ ግዢ ሃላፊዎች በፖሊስ እየተፈለጉ ሲሆን፤ መጀመሪያ ላይ የተያዙትን ጨምሮ እስካሁን 13 ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር እንደዋሉ ተገልጿል፡፡ ተጨማሪ ተጠርጣሪዎች ይኖሩ እንደሆነ የተጠየቁት አቶ ጠይብ፣ ጉዳዩ ከእቃ ግዢና ኪራይ ጋር በተያያዘ ስለሆነ አንዳንድ ባለሀብቶችንም ሊመለከት ይችላል ካሉ በኋላ፣ እስካሁን ግን እንደሌለ ተናግረዋል፡፡ የኦሮሚያ ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ዘንድሮ ከከፈታቸው 250 መዝገቦች መካከል፣ 150 ያክሉ ላይ ውሳኔ እንደተሰጠባቸው አቶ ጠይብ ጠቅሰው፣ ተከሳሾች ከ4 ወር እስከ 18 ዓመት የሚደርስ የእስር ቅጣቶችና ተጨማሪ የገንዘብ መቀጮ ተፈርዶባቸዋል ብለዋል፡፡ ኮሚሽኑ በፍ/ቤት ውሳኔ አማካኝነት ከለአራት አመታት ባደረገው ግምገማና በደረሰው ጥቆማበኦሮሚያ ሚሊዮን ብር በላይ ገንዘብ ወደ መንግስት ካዝና እንዲገባ መደረጉን የገለፁት አቶ ጠይብ በሌሎች የክልሉ መስሪያ ቤቶች ላይ ምርመራው እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና
  • ለአንድ አመት የታሰሩት እንዲፈቱ ጠይቀዋል  
  •    የሼኩ ግድያ ድራማ ነው ብለዋል

በአዲስ አበባ አንዋር መስጊድ “የታሰሩ ይፈቱ” የሚል ተቃውሞ ባለፈው ሳምንት አርብ መካሄዱ የሚታወስ ሲሆን፣ በትናንትናው እለት በበኒ መስጊድ ብዙ ህዝብ በተገኘበት ሰፊ ተቃውሞ ታይቷል፡፡ ተቃውሞው፤ ታሳሪዎች አንድ አመት እንደሞላቸው ምክንያት በማድረግ የተካሄደ ነው ተብሏል፡፡ መፍትሔ አፈላላጊ በሚል ስያሜ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ የኮሚቴ አባላት፤ በሽብርተኝነት ክስ ቀርቦባቸው ከታሰሩ አንድ አመት የሞላቸው ሐምሌ 14 እንደሆነ የገለፁት ተቃዋሚዎቹ፤ “በአንድነታችን እንቀጥላለን” ከሚል መልዕክት ጋር በኢንተርኔት የተቃውሞ ጥሪ አስተላልፈው እንደነበር ተናግረዋል፡፡

ትናንት ቀትር ላይ ወደ ተክለሃይማኖትና ወደ ኩርቱ ህንፃ አቅጣጫ እንዲሁም ባንኮ ዲሮማ ድረስ ባሉት መንገዶች በርካታ ህዝብ በመስጊዱ ዙሪያ ተሰብስቦ ተቃውሞ ተስተጋብቷል፡፡ የታሳሪዎችን ፎቶ ያነገቡ ተቃዋሚዎች “ድምፃችን ይሰማ”፣ “የታሰሩት ይፈቱ”፣ “የዘገየ ፍትህ እንደተነፈገ ይቆጠራል”፣ “የሼሁ ግድያ ድራማ ነው” ብለዋል፡፡ ትላንት በተካሄደው ተቃውሞ በርካታ አድማ በታኝ ፖሊሶች በአንዋር እና በበኒ መስጊድ የነበሩ ሲሆን የሃይማኖት ስርዓቱ ያለ እንከን እንደተካሄደና ተቃውሞውም በሰላም እንደተጠናቀቀ ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

የቤኒሻንጉል ተፈናቃዮች አሁንም በችግር ላይ ናቸው” (መኢአድና ሠማያዊ ፓርቲ)

ከቤኒሻንጉል ክልል ተፈናቅለው ከነበሩት የአማራ ክልል ተወላጆች ጋር በተያያዘ የክልሉን የስራ ሃላፊዎችና መንግስትን ለመክሰስ፣ ሰማያዊ ፓርቲና መላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ጥብቅና ያቆሟቸው አለም አቀፍ የህግ ባለሙያው ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማሪያም፤ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃ/ማሪያም ደሳለኝ ግልፅ ደብዳቤ መፃፋቸው ተገለፀ፡፡ ሁለቱ ፓርቲዎች ከትናንት በስቲያ ከሠዓት በኋላ በሠማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት በጋራ በሠጡት መግለጫ፤ ተፈናቃዮቹ አሁንም ችግር ላይ መሆናቸውን፣ ልጆቻቸው ትምህርት ማቋረጣቸውን፤ በሚዲያ እንደሚነገረው ወደ ቀድሞ ኑሯቸው አለመመለሳቸውንና በአጠቃላይ ችግር ላይ መሆናቸውን በማስረጃ በማስደገፍ፣ የጉራፈርዳንና የቤኒሻንጉል ተፈናቃዮችን በማነጋገርና በበርካታ መረጃዎች የተደገፉ ዶክሜንቶችን በማያያዝ ዶ/ር ያዕቆብ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የላኩትን ደብዳቤ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት ፈርሞ መቀበሉንም ፓርቲዎቹ ገልፀዋል፡፡

የሠማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት እንደተናገሩት፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ችግሩን በፓርላማ ቀርበው ማመናቸውን፣ ድርጊቱን ፈፅመዋል የተባሉት የክልልና የወረዳ ስራ አስፈፃሚዎች ከስራ መሰናበታቸውን፣ ተፈናቃዮቹ ወደነበሩበት ተመልሠው በሠላም እየኖሩ እንደሆነ የገለፁ ቢሆንም እውነታው ግን ከዚህ በተቃራኒው መሆኑን ዶ/ር ያዕቆብ ከተፈናቃዮች ጋር በመነጋገር ማረጋገጣቸውን ጠቁመው፣ ጉዳዩ ወደ ፍ/ቤት ከመሄዱ በፊት ጠቅላይ ሚኒስትሩ አፋጣኝ ምላሽ እንዲሠጡ ዶ/ር ያዕቆብ ለጠ/ሚኒስትሩ በላኩት ደብዳቤ አስታውቀዋል፡፡ ዶ/ር ያዕቆብ፤ አፋጣኝ ምላሽ ያሻቸዋል ያሏቸውን አራት ዋና ዋና ነጥቦች በደብዳቤያቸው ላይ ያሰፈሩ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ ተፈናቃዮቹ ወደ ቀድሞ ቦታቸው በመንግስት ወጪ ተመልሠው መሬታቸው፣ የንግድ ተቋሞቻቸውና ቤት ንብረታቸው በአስቸኳይ እንዲመለስላቸው፣ ተፈናቃዮቹ ለደረሰባቸው ቁሳዊ ጉዳት፣ አካላዊና ሞራላዊ እንግልት መንግስት ተመጣጣኝ ካሳ እንዲከፍላቸው የሚመለከታቸውን አካላት እንዲያዝዙ፣ በቤኒሻንጉል የሚኖሩ የማንኛውም ብሄር ተወላጆች ተመሳሳይ ወንጀል እንዳይፈፀምባቸው ጥበቃ እንዲደረግላቸው እና ተዋዶና ተፋቅሮ የሚኖረውን ህዝብ በመከፋፈል የማፈናቀል ድርጊት የፈፀሙ የመንግስት ባለስልጣናት ህግ ፊት ቀርበው ቅጣት እንዲያገኙ ውሳኔ እንዲያሳልፉ የሚሉት ነጥቦች ተቀምጠዋል፡፡

መንግስት ወንጀለኞች ያላቸውን የወረዳ ስራ አስፈፃሚዎች ከስራ ማሠናበቱንና ጉዳያቸው በፍ/ቤት እየታዩ ያለ ባለስልጣናት እንዳሉ፣ ተፈናቃዮቹም ወደ ቀድሞ ህይወታቸው ተመልሠዋል እየተባለ ነው የተፈናቃዮቹን ጉዳይ ለምን በተደጋጋሚ ማንሳት ፈለጋችሁ በሚል ከጋዜጠኞች ለተነሳው ጥያቄ “ኢትዮጵያ ውስጥ ፖለቲከኛ ለመሆን በርካታ ምክንያቶች አሉ” ያሉት ኢ/ር ይልቃል፤ ነገር ግን ተፈናቃዮች አሁንም በችግር ላይ ናቸው ቤት ንብረታቸውን የአካባቢው ባለስልጣናት ተቀራምተውት በክረምት ሜዳ ላይ የወደቁ አሉ፣ በፋሲካ በዓል ቤታቸው የተቃጠለባቸው ተፈናቃዮች አሉ፣ ወደ ቀድሞ ቦታቸው ያልተመለሱትም በርካቶች ናቸው ካሉ በኋላ “ጠበቃችን ዶ/ር ያዕቆብ ይህንን ጉዳይ ከተፈናቃዮቹ በተጨባጭ አረጋግጠዋል” ሲሉም አክለዋል፡፡ የመኢአድ ዋና ፀሀፊ አቶ ተስፋዬ ታሪኩ በበኩላቸው፤ የጉራፈርዳ ተፈናቃዮች በችግር ላይ ለመሆናቸው ጋዜጣዊ መግለጫውን እስከሠጡበት ሰዓት እንኳን መረጃዎች እየደረሷቸው እንደሆነ ገልፀው፣ በጠበቃው ዶ/ር ያዕቆብ በኩል ደብዳቤ መፃፋችን ጉዳዩ በፍ/ቤት እልባት እስኪያገኝ አስቸኳይ መፍትሄ እንዲሠጣቸው ነው ብለዋል፡፡

ችግሩ መቆም ያልቻለው ከመረጃ እጥረት ይሆናል በሚል ምን ያህል ሰዎች በችግር ላይ እንዳሉ፣ ቤት ንብረታቸውን ቆጥረው የተመዘገቡበት መረጃ ከየምርጫ ጣቢያው የወሠዱትን ካርድ መልሠውና ንብረታቸውን አስመዝግበው እንዲወጡ በሀላፊዎች ፊርማና በመንግስት ማህተም የታዘዙበት ደብዳቤና በርካታ ዶክሜንቶችን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ከደብዳቤው ጋር አያይዘው መላካቸውም ተገልጿል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአገሪቱ መሪ እንደመሆናቸው ችግሩንም በፓርላማ ቀርበው ማመናቸው እንደ ማስረጃ ተቆጥሮ የአገሪቱ የስራ አስፈፃሚ ከፍተኛ አካል በመሆናቸው ስለሚከሰሱ “መረጃው የለኝም አላየሁም” እንዳይሉ ታስቦ፣ ዶክሜንቱ እንደተላከላቸውም በፓርቲዎቹ ተገልጿል፡፡ ወደ ክስ ከሄዳችሁ ደብዳቤው ለምን አስፈለገ? ጠ/ሚኒስትሩ ምላሽ ከሠጡስ ክሱ ይቆማል ተብሎ ከጋዜጠኞች ለተነሳው ጥያቄ “ችግሮች መፍትሄ ካገኙ ክሱ ቀድሞውኑ ለምን ያስፈልጋል” ያሉት ኢ/ር ይልቃል፤ “መንግስት ይህን ወንጀል የፈፀሙትን አስሬያለሁ ከስራ አሠናብቻለሁ” የሚለው ጉዳዩ አለም አቀፍ ስለሆነበት ውጥረቱን ለማርገብ ነው ብለዋል፡፡ ምላሽ ካላገኛችሁ በትክክል ክስ መቼ ትጀምራላችሁ ለሚለውም፤ ወንጀሉ የይርጋ ጊዜ ስለሌለው ዶ/ር ያዕቆብ ለህክምና ከሄዱበት አሜሪካ ሲመለሱ ይጀመራል፣ በአገር ውስጥ ፍ/ቤት ካልተሳካ ጉዳዩ ወደ አለም አቀፍ ፍርድ ቤቶች ያመራል ብለዋል - የመኢአድ ዋና ፀሀፊ አቶ ተስፋዬ ታሪኩ፡፡ እስካሁንም በጉራፈርዳ ከሚኖሩ 78ሺህ የአማራ ተወላጆች መካከል 21ሺህ ያህሉ መፈናቀላቸውንና በቤኒሻንጉልም ከአምስት ሺህ በላይ ተፈናቃዮች አፋጣኝ መፍትሔ እንደሚሹ የፓርቲው አመራሮች ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

የስነምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን የምርመራ ቡድን፤ በእነ ዳዊት ኢትዮጵያ መዝገብ ስር ተጠቃለው የሚገኙት ከፍተኛ ባለሀብቱ አቶ ማሞ ኪሮስ በሌላ መዝገብ ተጠርጥረው ከሚገኙ የጉምሩክና ገቢዎች ባለስልጣን ከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር ባቋቋሙት “ልማት ለእድገት” የተባለ ድርጅት ላይ ምርመራ እያካሄደ መሆኑን ገለፀ፡፡ ድርጅቱን የሚገምት የባለሙያዎች ቡድንም ተቋቁሟል፡፡ አቶ ማሞ በስራ አስኪያጅነት ይመሩታል የተባለው ይህ ድርጅት በተለያየ ጊዜ ከህግ አግባብ ውጪ እቃዎችን ከውጭ ሀገር ያስገባ እንደነበር ለፍርድ ቤት ያስረዳው የምርመራ ቡድኑ፤ እስካሁን ይህን የሚያስረዱ ሰነዶች መሰባሰባቸውንና 4 ምስክሮች መቆጠራቸውን ለፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 2ኛ ወንጀል ችሎት አመልክቷል፡፡ በእኚሁ ባለሀብት በህገወጥ መንገድ ወደ ሀገር ውስጥ እንዲገቡ ተደርገዋል የተባሉ 22 ኮንቴነር እቃዎች ሞጆ በሚገኘው ደረቅ ወደብ ተይዘው ምርመራ እየተከናወነ እንደሆነም ተጠቁሟል፡፡

ከትላንት በስቲያ በዚሁ መዝገብ ስር የሚገኙትን የጉምሩክ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎችና ሠራተኞች እንዲሁም ባለሀብቶችን ጉዳይ ችሎቱ የተመለከተ ሲሆን የምርመራ ቡድኑም ቀደም ሲል በተሰጠው የ10 ቀን የምርመራ ጊዜ ውስጥ ያከናወናቸውንና ይቀሩኛል ያላቸውን ስራዎች በዝርዝር በመግለጽ፣ ለ7ኛ ጊዜ የጠየቀው የምርመራ ጊዜ ተፈቅዶለታል፡፡ በዚህ መዝገብ ከአቶ ማሞ ኪሮስ በተጨማሪ አቶ ዳዊት ኢትዮጵያ፣ አቶ ማሞ አብዱ፣ አቶ አሸብር ተሰማ፣ ፍፁም ገ/መድህን፣ እንዲሁም አቶ አበበለኝ ተስፋዬ የተካተቱ ሲሆን በተጠርጣሪዎቹ ላይ የምርመራ ቡድኑ በተሰጠው የ10 ቀን ጊዜ ውስጥ ከታክስና ቀረጥ ስወራ ጋር በተያያዘ በሁሉም ተጠርጣሪዎች ላይ ሰነድ ተሰባስቧል፣ በ3 ኩባንያዎች ላይ የሚደረገው የኦዲት ስራም ተጠናቋል፡፡

በህገወጥ መንገድ የተገኘ ገንዘብን ህጋዊ አድርጐ መያዝ በሚለው በአቶ አሸብር ተሰማ ላይ የሰው ማስረጃ እየተሰባሰበና ክትትል እየተደረገ ነው፣ ምንጩ ያልታወቀ ሃብትን በተመለከተ በአቶ ዳዊት ኢትዮጵያ፣ በአቶ ማሞ አብዱ፣ በአቶ አሸብር ተሰማ እና በአቶ አበበልኝ ተስፋዬ ላይ ከክ/ከተሞች፣ ከባንክ፣ ከትራንስፖርት ቢሮዎች እንዲሁም ከክልሎች ማስረጃ ተሰባስቧል ብሏል፡፡ በሌላ በኩል የምርመራ ቡድኑ በዚህ መዝገብ ይቀሩኛል ብሎ የ14 ቀን ቀጠሮ የጠየቀባቸው ስራዎች፡- የቀሪ ሁለት ኩባንያዎችን ኦዲት ማጠናቀቅ፣ የታክስ ልዩነት በመፍጠር እቃዎችን አስገብተዋል በተባሉት ላይ የዘጠኝ ምስክሮችን ቃል መቀበል፣ በአቶ ማሞ ኪሮስ እና በባለስልጣናቱ ተቋቋመ ከተባለው ድርጅት ጋር በተያያዘ ተጨማሪ 5 ምስክሮችን ቃል መቀበልና ንብረቱን በባለሙያ አስገምቶ ሪፖርቱን መቀበል፣ የባለሙያ ምስክርነት ቃል መቀበል፣ በህገወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ ህጋዊ አስመስሎ መያዝን በተመለከተ ከአዋሣና ጐንደር የንብረት ግምት ሪፖርትና የምስክር ቃል ተጠናቆ እንዲመጣ መከታተል የሚሉት ናቸው። በመርማሪ ቡድኑ ሪፖርት ላይም ተጠርጣሪዎችና ጠበቆቻቸው ከዚህ ቀደም በነበረው ችሎት ያቀረቡት መከራከሪያ እንዲመዘገብላቸው በመጠየቅና የየግል ምክንያታቸውን በማቅረብ፣ የዋስትና መብታችን ተከብሮ ጉዳያችንን በውጭ ሆነን እንድንከታተል ይፈቀድልን ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ የመርማሪ ቡድኑም በሰጠው ምላሽ፤ በሪፖርቱ እንደተገለፀው ቀሪ የምርመራ ስራዎች ስላሉ፣ ተጠርጣሪዎች በዋስ ቢወጡ ያላቸውን ስልጣንና ሃብት በመጠቀም ምስክሮችና ሊያባብሉ፣ ሰነዶችን ሊያሸሹ ይችላሉ በዚህም ፍትህ ሊጓደል ይችላል በሚል የዋስትና ጥያቄውን ተቃውሟል፡፡

የግራ ቀኙን የቃል ክርክር ሲያደምጥ የቆየው ችሎቱም፤ የመርማሪ ቡድኑ ቀሪ ስራዎች እንዳሉት በመገንዘብ፣ የተጠርጣሪዎችን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ በማድረግ ከተጠየቀው የ14 ቀን ቀጠሮ ውስጥ 10 ቀን በመፍቀድ መዝገቡን ለሐምሌ 29ቀን2005 ቀጥሯል፡፡ በተጨማሪም ምርመራው በተገቢ ፍጥነትና ጥራት እንዲከናወን ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ በእለቱ ፍርድ ቤቱ የእነ አቶ አምባው ሰገድ አብርሃን መዝገብ 12 ተጠርጣሪዎች የተካተቱበት ተመልክቷል- አቶ አምባው ሰገድ አብርሃ፣ ተክለአብ ዘረአብሩክ፣ ያደሳ ሚደቅሳ፣ እሸቱ ግረፍ፣ ጌታሁን ቱጂ፣ መላኩ ግርማ፣ አስፋው ስዩም፣ ጌታነህ ግደይ፣ ዮሴፍ አዲዮ፣ በእግዚአብሔር አለበል፣ ዘለቀ ልየው እና መሐመድ ሃሰን ፡፡ የምርመራ ቡድኑ በዚህ መዝገብ በተጠረጠሩት ላይ በተሰጠው 10 ቀን ውስጥ ያከናወናቸውን ተግባራት የዘረዘረ ሲሆን ለጠቋሚ የሚከፈልን አበል ለራስ በማድረግ የተጠረጠሩት አቶ አምባው ሰገድ አድራሻ ላይ የሚመሰክሩ ግለሰቦች አድራሻ መገኘቱን፤ ሞጆ፣ አዳማ፣ ድሬደዋ፣ ሚሌ የተላከው የምርመራ ቡድን እንደቅደም ተከተላቸው ከ2-8 እንዲሁም በ11ኛ ተጠርጣሪዎች ላይ ሰነዶች መሰብሰቡን፣ በአዋሽ መቅረጫ ጣቢያ በህገወጥ መንገድ ሲገቡ የተያዙ ካሜራዎችን በተመለከተ በአቶ እሸቱ ግረፍ እና በአቶ አስፋው ስዩም ላይ የሰነድ ማስረጃዎች መሰብሰባቸውን፣፣ ተገቢው ቀረጥ ሳይከፈልባቸው የገቡ እቃዎችን በተመለከተ የ3 ኩባንያዎች ኦዲት መጠናቀቁን፣ በድሬደዋ የተያዙ የኮንትሮባንድ ንብረቶችን ተመሳጥሮ መሸጥን በተመለከተ ጉዳዩ በሚመለከታቸው በአቶ ጌታሁን ቱጂ እና መሐመድ ሃሰን ላይ መረጃ ተሰባስቦ የምስክሮች ቃል መቀበሉን፣ በቦሌ በኩል በህገወጥ መንገድ የገቡ የኮንትሮባንድ እቃዎችን በተመለከተ በአቶ ዘለቀ ልየው ላይ የ1 ምስክር ቃል ማግኘቱን፣ ምንጩ ያልታወቀ ሃብት ይዞ መገኘትን በተመለከተ ከክፍለከተሞች ባንኮችና ክልሎች እንዲሁም ከትራንስፖርት ቢሮዎች ሰነድ መሰብሰቡንና ንብረታቸው ላይ ለመድረስም ክትትል እየተደረገ መሆንኑ ጠቁሟል፡፡

በሌላ በኩል የሚቀሩ ስራዎች ተብለው በመርማሪ ቡድኑ የተዘረዘሩት የጠቋሚ አበልን ለራስ አድርጐ መጠቀምን በተመለከተ በአቶ አምባው ሰገድ ላይ የ5 ምስክሮችን ቃል መቀበል፣ ምንጩ ያልታወቀ ሃብትን የዋጋ ግምት ማውጣት፣ ከቀረጥ ስወራ ጋር በተያያዙ ደጋፊ ሰነድ ማስረጃ ማቅረብና የ2 ምስክሮችን ቃል መቀበል፣ የኦዲት ምርመራ ደጋፊ ሰነድ ማቅረብ እና የ2 ኩባንያዎችን ኦዲት ማጠናቀቅ፣ የቀረጥ ልዩነት መፍጠር በሚለው የ9 ምስክሮችን ቃል መቀበል፣ በድሬደዋ የተያዙ ኮንትሮባንድ ንብረቶችን በተመለከተ የምስክሮችን ቃል መቀበል እና ክትትል ማድረግ፣ በቦሌ የገቡ የኮንትሮባንድ እቃዎችን በተመለከተ የ2 ምስክሮች ቃል መቀበል የሚሉት ናቸው፡፡ እነዚህን ቀሪ ስራዎች ለማከናወንም መርማሪ ቡድኑ ተጨማሪ የ14 ቀን ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ ተጠርጣሪዎችና ጠበቆች በበኩላቸው፤ ተመሳሳይ የምርመራ ሪፖርቶች ናቸው የሚቀርቡት፣ የሚፈለጉት ሰነዶች በሙሉ ተሰባስበዋል የሚሉና ሌሎች የየግል ምክንያቶቻቸውን አቅርበው ጉዳያቸውን በዋስ ሆነው እንዲከታተሉ ጠይቀዋል፡፡ የመርማሪ ቡድኑ በበኩሉ፤ በሰጠው ምላሽ የሚከናወኑት የምርመራ ስራዎች ተከታታይነት ያላቸው ናቸው፣ ቡድኑም በአግባቡ ጊዜውን እየተጠቀመ እየሰራ ነው፣ ተጠርጣሪዎች በዚህ ሁኔታ በዋስ ቢለቀቁ ምስክሮችን በማባበል፣ ማስረጃዎችን በመወሰር የፍትህ ሂደቱ ላይ አሉታዊ ተጽእኖ ሊፈጥሩ ስለሚችሉ የዋስ መብታቸውን እቃወማለሁ ብሏል፡፡ የግራ ቀኝ የቃል ክርክሩን ሲያዳምጥ የቆየው ችሎቱም፤ የተጠርጣሪዎችን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ በማድረግ የምርመራ ስራው በተገቢው መንገድ ያከናውን ዘንድ የ10 ቀን ቀጠሮ ፈቅዶ መዝገቡን ለሐምሌ 29ቀን2005ዓ.ም ቀጥሯል፡፡

Published in ዜና
Page 3 of 13