ዶ/ር መረራ የ11 ወር፣ ዶ/ር ዳኛቸው የ8 ወር ደሞዝ አልተከፈለንም አሉ
አሁንም  በዩኒቨርሲቲው እያስተማሩ መሆናቸውን ገልጸዋል

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካል ሣይንስ መምህሩ ዶ/ር መረራ ጉዲና እና የፍልስፍና ምሁሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሠፋ በመኖሪያ ቤትና  በደሞዝ ጉዳይ ከዩኒቨርሲቲው አስተዳደር ጋር እየተወዛገቡ ነው፡፡ ዶ/ር መረራ ጉዲና የ11 ወር ደሞዛቸውን ተከልክለው ለ12 አመት ከኖሩበት የዩኒቨርስቲው ንብረት የሆነ መኖሪያ ቤት በ15 ቀናት ውስጥ እንዲለቁ የታዘዙ ሲሆን ዶ/ር ዳኛቸው አሠፋም የ8 ወር ደሞዛቸው ሳይከፈላቸው፣ ለ 7 አመት ከኖሩበት ቤት እንዲለቁ ደብዳቤ ተጽፎላቸዋል፡፡   ለ28 አመታት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ማስተማራቸውን የሚገልፁት ዶ/ር መረራ፤ ከወራት በፊት የዩኒቨርሲቲው የበላይ አስተዳደር ከዩኒቨርስቲው ጋር ያላቸው ውል መቋረጡን ቢያሳውቃቸውም የፖለቲካ ሣይንስ የሚያስተምሩበት የሶሻል ሳይንስ ኮሌጅ ውሉን እንዳላቋረጠና የ2 አመት ኮንትራት እንዳላቸው ይናገራሉ፡፡ የዩኒቨርስቲው የበላይ አመራር ግን የማስተማር ስራቸውን
እንዳቆሙ አድርጐ ለ12 አመት ከኖሩበት መኖሪያ ቤት በ15 ቀናት ውስጥ እንዲለቁ ደብዳቤ እንደፃፈላቸው ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው ለቤቱ አገልገሎት ያልከፈሉትን 2300 ብር እዳ እንዲከፍሉም በደብዳቤው አሳስቧል፡፡ “ቤቱን ለመልቀቅ ሌላ ቤት እያፈላለግሁ ነው” ያሉት ዶ/ር መረራ፤ ነገር ግን ዩኒቨርሲቲው ለ11 ወራት ያስተማርኩበትን ደሞዜን አልከፈለኝም ሲሉ ያማርራሉ፡፡ አሁንም እያስተማርኩ ነው ያሉት ምሁሩ፤ የዩኒቨርሲቲው አስተዳደር ነው እንጂ የማስተምርበት ኮሌጅ የኮንትራት ውሌን አላቋረጠም፤ ከኮሌጁ ጋርም የ2 ዓመት የኮንትራት ውል አለኝ” ብለዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው የ11 ወራት ደሞዛቸውን እንዲከፍላቸው ለፍ/ቤት አቤት ለማለት በዝግጅት ላይ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡  ምህራንን የመቅጠርም ሆነ የማባረር ስልጣን የበላይ አመራሩ ሳይሆን የኮሌጁ ነው ያሉት ዶ/ር መረራ፤ የዩኒቨርሲቲው የበላይ አመራር ጣልቃ ገብቶ ነው ደሞዜ የታገደው ብለዋል፡፡ የበላይ አመራሩ ህጋዊ ተግባር እንዳልፈፀመ በፅሁፍ ለዩኒቨርሲቲው የቦርድ አመራሮች ማሳወቃቸውንም ዶ/ሩ ተናግረዋል፡፡ “ከባድ የማግለል ተግባር እየተፈፀመብኝ ነው” የሚሉት ምሁሩ፤ የፕሮፌሰርነት ማዕረጌንም አላግባብ ተከልክያለሁ፤ የሲቪል ሰርቪስ ፍ/ቤት ለሚባል አካልም ጉዳዩን አመልክቼ ምላሽ እየተጠባበቅሁ ነው ብለዋል፡፡ በዩኒቨርሲቲው ለ7 ዓመት በፍልስፍና ትምህርት ክፍል መምህርነት ያገለገሉት ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋም  የዩኒቨርሲቲው ንብረት ከሆነው መኖሪያ ቤት ያለባቸውን 3300 ብር እዳ ከፍለው፣ በ15 ቀናት ውስጥ እንዲለቁ መታዘዛቸው የሚታወስ ሲሆን ዶ/ር ዳኛቸው ለዩኒቨርሲቲው የመልስ ደብዳቤ ፅፈው ምላሹን እየተጠባበቁ እንደሆነ  ታውቋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው ቤቱን በተመለከተ አፋጣኝ ምላሽ ካልሰጣቸው ለቀጣይ ሦስት ወራት ቤቱን እንደማይለቁ ተናግረዋል፡፡
“አንድ ባለስልጣን በጡረታ ሲገለል ሙሉ ጥቅማ ጥቅሙ ተከብሮለት ቢሆንም አንድ ትውልድ የሚቀርፅ የዩኒቨርሲቲ መምህር እንዲሁ በቀላጤ ከምትኖርበት ውጣ መባሉ ያሳዝናል” ብለዋል ምሁሩ፡፡
የ8 ወራት ደሞዛቸውም እንዳልተከፈላቸውና እስካሁንም ከዩኒቨርሲቲው ህጋዊ በሆነ ደብዳቤ የስራ ውላቸው ስለመቋረጡ የደረሳቸው መልእክት እንደሌለ የሚናገሩት ዶ/ር ዳኛቸው፤ የማስተማር ስራቸውንም ሙሉ ለሙሉ እንዳላቆሙ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ በሌላ በኩል “የዳኛቸው ሃሳቦች” በሚል ርዕስ በታተመው መፅሃፍ “ሃሳቤን ተዘርፌያለሁ” ያሉት የፍልስፍና ምሁሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፤ በመፅሃፉ አዘጋጅ መሃመድ ሃሰን እና በአከፋፋዩ አቶ አስራት አብርሃ ላይ በከፍተኛው ፍ/ቤት ትናንት ክስ መመስረታቸውን አስታውቀዋል፡፡ የመፅሃፉ አዘጋጅ መሃመድ ሃሰን ይቅርታ መጠየቁን የጠቆሙት ዶ/ር ዳኛቸው፤ ሁለቱንም ግለሰቦች በወንጀል መክሰስ ያስፈለገው ለሌላውም መማሪያ እንዲሆን ነው ብለዋል፡፡ በመፅሃፉ 95 በመቶ
የሚሆነው ሃሳብ በተለያዩ ጊዜያት የተናገሯቸው፣ ያስተማሯቸው፣ በተለያዩ መድረኮች ላይ ገለፃ የሰጡባቸውና በሰነድና በተለያዩ ፅሁፎች የተቀመጡ መሆናቸውን ያብራሩት ዶ/ር ዳኛቸው፤ ለክሱ ማስረጃነትም እነዚሁ ሰነዶች ተያይዘው መቅረባቸውን ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

ማኅበረ ቅዱሳንን በመወንጀል ‹‹ወጣቶቹን ሰብስባችሁ እሰሩልን›› ያሉ አስተዳዳሪዎች የፖሊስ እና
የደኅንነት አካላትን በተባባሪነት ወቀሱ‹‹ማኅበረ ቅዱሳንን እንደተቋም መወንጀል አትችሉም፤ ፖሊስ የእናንተ ብቻ አይደለም፤ መጀመሪያ ራሳችኹን ፈትሹ›› /ዶ/ር ሺፈራው ተክለ ማርያም
     በሙስና መንሰራፋት፣ በመልካም አስተዳደር እና በፍትሕ ዕጦት ሳቢያ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እየተደረገ ካለው የአገልጋዮች እና የምእመናን መነሣሣት ጋር በተያያዘ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የቤተ ክርስቲያኒቱን አካላት ማነጋገር ጀመረ፡፡ ብልሹ የሰው ኃይል አስተዳደር እና የፋይናንስ አሠራር በተከታዩ ዘንድ የሚፈጥረው የተከማቸ ቅሬታ፣ የሃይማኖት ተቋማቱ እምነት እንዲያጡ ምክንያት እየኾነ እንዳለ በሥልጠና ሰነዶቹ የሚገልጸው ሚኒስቴሩ፣ በቅርቡም የወሳኝነትና የተሳትፎ ድርሻ ያላቸው የተለያዩ የቤተ ክርስቲያኒቱ የአስተዳደር እና የአገልግሎት አካላት የሚሳተፉበት ተከታታይ ውይይት እንደሚያካሒድ ተጠቁሟል፡፡በሚኒስቴሩ ጥያቄ፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የተመረጡ የአድባራት አስተዳዳሪዎች ከትላንት በስቲያ ከቀትር በኋላ ከሚኒስትሩ ዶ/ር ሺፈራው ተክለ ማርያም እና ከሚኒስትር ዴኤታው አቶ ሙሉጌታ ውለታው ጋር የውይይቱ ቅድመ ዝግጅት ነው የተባለ ምክክር አድርገዋል፡፡በዋና ሥራ አስኪያጁ ሊቀ ማእምራን የማነ ዘመንፈስ ቅዱስ የተመሩ የኻያ አምስት አድባራት አስተዳዳሪዎች በተካፈሉበት በዚኹ ምክክር፣ ‹‹በማኅበራት ሰላማችንን እያጣን ነው፤ ሰንበቴ ሲከበን እናንተም የላችኹም፤ መንግሥትም የለም፤ አልደገፋችኹንም፤ አልረዳችኹንም›› የሚሉ ክሦች እና አቤቱታዎች ከአንዳንድ አለቆች መቅረቡ ተጠቅሷል፡፡ካለፈው ሚያዝያ ወር መጨረሻ ጀምሮ የሀገረ ስብከቱ ሰንበት ት/ቤቶች ፥ ሙስና እንዲወገድ፣ መልካም አስተዳደርና ፍትሕ እንዲሰፍን፣ እምነትና ሥርዐት እንዲጠበቅ በሰልፎችና በስብሰባዎች
የሚያካሒዱት እንቅስቃሴም ‹‹ማኅበረ ቅዱሳን ልብሱን ለውጦ የመጣበት ነው›› ብለዋል - አስተዳዳሪዎቹ፡፡
የሰንበት ት/ቤት አባላቱ የመለያ ልብሶቻቸውን (ዩኒፎርሞቻቸውን) ለብሰው በመውጣት በሚያደርጓቸው ሰልፎችና ስብሰባዎች መንግሥት የጸጥታ ርምጃ ሳይወስድ በዝምታ መመልከቱን የተናገሩት አስተዳዳሪዎቹ፣ የፖሊስ እና የደኅንነት አካላትን በተባባሪነት በመውቀስ፣ ‹‹ወጣቶቹን እሰሩልን›› ብለው ሲጠይቁ ተሰምተዋል፡፡የቤተ ክርስቲያንን ሀብት ለግላቸው በማካበት ከገቢያቸው በላይ የሚኖሩ አለቆች በሥነ ምግባርና በፀረ ሙስና ኮሚሽን እየተመረመሩ በሀገሪቱ ሕግ እንዲጠየቁ የሰንበት ት/ቤቶቹ የሚጠይቁ ሲኾን
ዋና ሥራ አስኪያጁ እና አንዳንድ አለቆች በአንፃሩ፣ ‹‹ዶልፊን እና ሃይገር የሚያቆሙ ናቸው፤ ቢዝነስ አድርገውታል” በማለት ይከሷቸዋል፡፡በምክክሩ ወቅት ብሶት ነው የሚያስጮኸኝ በማለት በከፍተኛ ድምፅ የተናገሩ አንድ አስተዳዳሪ፣ “ማኅበረ ቅዱሳን አባላቱን የሰንበት ት/ቤት ዩኒፎርም አስለብሶ መውጣት ጀምሯል፤ ሕንፃውን ከየት አምጥቶ ነው ያቆመው?” ሲሉ በሰንበት ት/ቤቶቹ መነሣሣት ማኅበሩን ተጠያቂ አድርገዋል፡፡ “ወጣቱን ዩኒፎርም እያስለበሱ ይልካሉ” ያሉ የሌላ ደብር አስተዳዳሪም፤ “እንዴት አድርገን
መከላከል እንዳለብን አሠልጥኑን እንጂ ስለሰላም ምን ያደርግልናል” በማለት የሚኒስቴሩን
ሓላፊዎች አስደምመዋል ይላሉ የስብሰባው ተሳታፊዎች፡፡ፖሊስ እና የጸጥታ አካላት የሕዝብን ሰላም እና ደኅንነት የሚጠብቁ መኾናቸውን የተናገሩት ሚኒስትሩ ዶ/ር ሺፈራው ተክለ ማርያም፣ ‹‹ፖሊስ ለእናንተ ብቻ ነው እንዴ?›› ሲሉ አለቆቹን ጠይቀዋቸዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን በሲኖዶስ ዕውቅና የተሰጠው ሕጋዊ ማኅበር መኾኑን ሚኒስትሩ ጠቅሰው፣ ችግር ያለባቸው ግለሰቦች ይኖራሉ እንጂ ማኅበር እያችሁ በጅምላ መጥራት የለባችኹም፤ ተቋሙን በጅምላ መፈረጅ ወንጀል ነው፤›› ብለዋል፡፡ ሀገረ ስብከቱን ጨምሮ አስተዳዳሪዎቹ በሚመሯቸው አድባራት መልካም አስተዳደርን በማስፈን ለምእመናንና ለሰንበት ት/ቤቶቹ ወጣቶች ምሳሌ መኾን እንደሚገባቸው የተናገሩት ሚኒስትሩ፣ ‹‹ሰው እሰሩ ያላችኹት ሌላ ችግር ነው የሚፈጥረው፤ የምናስረው ሰው የለም፤ መጀመሪያ ራሳችኹን ፈትሹ›› በሚል ለአለቆቹ የእሰሩልን ጥያቄ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በሚኒስቴሩ ዕቅድ መሠረት ይካሔዳል የተባለውና በቤተ ክርስቲያኒቱ ከሚታየው የአገልጋዮችና የምእመናን መነሣሣት ጋር የተገጣጠመው ይኸው የቅድመ ውይይት ምክክር፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ የአስተዳደር መዋቅር የወሳኝነት እና የተሳትፎ ድርሻ ያላቸውን የማኅበረ ካህናትን፣ የማኅበረ ምእመናንና የሰንበት ት/ቤቶች ተወካዮችን
ሊያካትት እንደሚገባው አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ፡፡በዘመናዊ አሠራር፣ በመልካም አስተዳደር እና በሰላም ጉዳዮች ላይ የሚያተኩረው ዋናው ውይይት፤ በሚቀጥሉት ኹለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ እንደሚጀመር የሚኒስቴሩ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ የውይይቱን አቅጣጫ ለማመቻቸት በሚል ከትላንት በስቲያ በሀገረ ስብከቱ ሓላፊዎች ከተመሩት የአድባራት አለቆች ጋር ከተካሔደው ምክክር ፍጻሜ በኋላ ‹‹ዘመናዊ አሠራር ዴሞክራሲዊነት እና ብዝኃነት›› በሚል ርእስ በሚኒስቴሩ የተዘጋጀ የመወያያ ሰነድ እንደተሰጣቸውም ንጮቹ ገልጸዋል፡፡

Published in ዜና

ሬዲዮ ጣቢያው ሊታገድ እንደሚችል ማስጠንቀቂያ ደርሶታል

    በዛሚ 90.7 ሬድዮ በሚተላለፈው የኢትዮፒካሊንክ ፕሮግራም በሚቀርበው “ውስጥ አዋቂ” የተሰኘ ዝግጅት በተደጋጋሚ ስሜ ጠፍቷል ያለው አርቲስት ዳንኤል ተገኝ፤ ለኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን አቤቱታ ማስገባቱን ተከትሎ ዛሚ ሬዲዮ እና ባለስልጣኑ እየተወዛገቡ ነው፡፡ በተለያዩ ፊልሞች እና የቴሌቪዥን ድራማዎች ላይ በመተወን የሚታወቀው አርቲስት ዳንኤል ተገኝ፤ በሬዲዮ ጣቢያው የሚተላለፈው ኢትዮፒካሊንክ ፕሮግራም ከ1 ዓመት ከ8 ወር በፊት ጀምሮ የስም ማጥፋት ዘመቻ እንደከፈተበት ይናገራል፡፡ “ወደ 6 በሚሆኑ ፕሮግራሞቻቸው ያልሆንኩትን ሆነ፣ ያላደረኩትን አደረገ እያሉ ስሜን ሲያብጠለጥሉ ቆይተዋል” የሚለው አርቲስቱ፤ በተደጋጋሚ ጉዳዩን ለብሮድካስት ባለስልጣን ማመልከቱንና ባለስልጣኑም የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ ለአዘጋጆቹ እንደፃፈ ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ ጉዳዩን በተመለከተ ከአርቲስቱ ተደጋጋሚ አቤቱታ የቀረበለት ብሮድካስት ባለሥልጣንም ከሁለት ሳምንታት በፊት በፕሮግራሙ “የውስጥ አዋቂ” ዝግጅት ላይ የእግድ ደብዳቤ ማውጣቱን የሚገልፀው አርቲስቱ፤ ጣቢያው እገዳውን ሳይቀበል ለአዘጋጆቹ ሽፋን እየሰጠ እግዱን ተግባራዊ ሳያደርግ ቀርቷል ብሏል፡፡ ለሁለተኛ ጊዜም የብሮድካስት ባለሥልጣን የስራ አመራሮች እና አቤቱታ አቅራቢውን ጨምሮ አርቲስት ዮሐንስ አፈወርቅ፣ አርቲስት በኃይሉ ከፍያለውና ጋዜጠኛ አብርሃም ግዛው እንዲሁም የአርቲስቱ ጠበቃ አቶ መልካሙ ሆነው በጉዳዩ ላይ ተሰብስበው መምከራቸውንና የብሮድካስት ባለሥልጣን አመራሮችም “ከዚህ በኋላ ህግን የማስከበር ጉዳይ የኛ ነው፤ ለኛ ተዉልን” እንዳሏቸው አርቲስቱ ለአዲስ አድማስ አብራርቷል፡፡ ነገር ግን ፕሮግራሙ አሁንም
እየተላለፈ ነው ብሏል፡፡ “ገና የአንተን ስም አጠፋዋለሁ፤ እዚህች ሃገር ላይ ሠርተህ አትኖርም” የሚል ዛቻና ማስፈራሪያ ሠንዝረውብኛል” ያለው አርቲስቱ፤ ጉዳዩ በብሮድካስት በኩል እልባት የማያገኝ ከሆነ ለጠቅላይ
ሚኒስትር ፅ/ቤት አቤቱታውን እንደሚያቀርብ፤ ወደ ፍ/ቤት ቀርቦም ክስ ለመመስረት እየተሰናዳ
መሆኑን ገልጿል፡፡ በጉዳዩ ላይ የፕሮግራሙን አዘጋጆች በስልክ ለማነጋገር ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ ባይሳካም የጣቢያው ስራ አስኪያጅ አቶ ዘሪሁን ተሾመ፤ በአርቲስቱ ምክንያት ከብሮድካስት ባለሥልጣን ጋር
የተፈጠረውን ውዝግብ ለመፍታት ከባለስልጣኑ የቦርድ ኮሚቴ ጋር እየተወያዩ መሆኑን ጠቅሰው፤
“ፕሮግራሙን አግዱ፤ አለበለዚያ እርምጃ ይወሰድባችኋል፤ እናግዳችኋለን” የሚል መልዕክት እንደመጣላቸውም ጠቁመዋል፡፡ ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ አንድን ፕሮግራም ካላገዳችሁ በሚል ጣቢያውን አግዳለሁ ማለቱ በህግ አግባብ  የማያስኬድ ነው ያሉት አቶ ዘሪሁን፤ አንድን የሚዲያ ተቋም የማገድ ስልጣንም የለውም ብለዋል፡፡ ጣቢያው በአሁን ሰዓት መደበኛ የእለት ተእለት ተግባሩን እያከናወነ መሆኑን አቶ ዘሪሁን ጠቁመው፣ “በሚዲያ ህጉ ተበደልኩ የሚል አካል ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት መውሰድ የሚችልበት የህግ
አግባብ እያለ አርቲስቱ በዚህ መንገድ መሄዱም ተገቢ አይደለም፤ እኛም ይሄን መሰሉን አካሄድ አናስተናግድም” ብለዋል፡፡ “አንድን ፕሮግራም በማያሳምን ምክንያት የምናግድ ከሆነ ተገቢ አይሆንም፤ ፕሮግራሙንም አናግድም” ብለዋል አቶ ዘሪሁን፡፡ ጉዳዩ የሚመለከታቸውን የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን ሃላፊዎችን በስልክ ለማነጋገርም ሆነ በአካል ቢሮአቸው ሄደን ለማግኘት ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ ስብሰባ ላይ ናቸው በመባላችን ሳይሳካልን ቀርቷል፡፡

Published in ዜና

 60 ዘጋቢ ፊልሞች ለተመልካች ይቀርባሉ
  ፌስቲቫሉ በክልል ከተሞችም ይቀጥላል
      በመላው ዓለም ከተሰሩ ምርጥ ዘጋቢ ፊልሞች የተመረጡ 60ዎቹ ለዕይታ የሚቀርቡበት “9ኛው አዲስ ኢንተርናሽናል ዘጋቢ ፊልም ፌስቲቫል” ትላንት በብሄራዊ ሙዚየም የቅርስ ጥናት እና ጥበቃ ባለስልጣን አዳራሽ ተከፈተ፡፡ ፌስቲቫሉ ለአምስት ቀናት እንደሚካሄድ የገለፁት የ“ኢንሺዬቲቭ አፍሪካ” ዋና ዲያሬክተር አቶ ክቡር ገና፤ በቀጣይ ዓመታት ፌስቲቫሉ የራሱን ውድድር አድርጎ ፊልሞችና ፊልም ሰሪዎችን ለመሸለም እንዲሁም ኢትዮጵያዊያን ፊልም ሰሪዎች በዘጋቢ ፊልሞች ስራ የተሻለ ተሳትፎ እንዲኖራቸው እንተጋለን ብለዋል፡፡ ፌስቲቫሉ የተከፈተው በሩት ኢሼል ዳይሬክተርነት በተሰራው “Shoulder Dancing” የተሰኘ ዘጋቢ ፊልም ነው፡፡ እስከ ሰኔ 9 በሚዘልቀው ፌስቲቫል፤ 60 የሚደርሱ ዘጋቢ ፊልሞች ለዕይታ የሚቀርቡ ሲሆን በአዲስ አበባ  በቅርስ ጥናትና ምርምር ማዕከል፤ በሀገር ፍቅር ትንሽዋ አዳራሽ፤ በብሪትሽ ካውንስል እና በአሊያንስ ኢትዮ ፍራንሲዝ ለተመልካቾች ይታያሉ፡፡ የፊልም ፌስቲቫሉ ሰኔ 19 እና 20 ደግሞ በአዳማ፤ ባህርዳር፤ ሃዋሳ እና መቀሌ  ከተሞች እንደሚካሄድ ተገልጿል፡፡
በዘንድሮው ፌስቲቫል በዓለማችን አበይት የመነጋገሪያ አጀንዳዎች ላይ ተመርኩዘው የተሰሩ ዘጋቢ ፊልሞች ተመርጠው መቅረባቸውን በጋዜጣዊ መግለጫው የተናገሩት አቶ ክቡር ገና፤ ከ10 በላይ የፊልም ዳይሬክተሮችን ከተለያዩ አገራት በመጋበዝ በፊልሞቹ ዙሪያ ከተመልካች ለሚነሱ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጡበት መድረክ መመቻቸቱንም ገልፀዋል፡፡ ባለፈው ዓመት ከ10ሺ በላይ ታዳሚ የነበረው አዲስ ኢንተርናሽናል ዘጋቢ ፊልም ፌስቲቫል፤ ዘንድሮ ደግሞ በፊልሞቹ ብዛት፤ በሚቀርቡት ዘጋቢ ፊልም ሰሪዎች የብቃት ደረጃና አይነት እንዲሁም በሚያገኘው ተመልካች ብዛት በአፍሪካ ግዙፉ ፌስቲቫል ይሆናል ተብሎ ይገመታል፡፡ በፌስቲቫሉ ላይ ለመሳተፍከመላው ዓለም 500 ፊልሞች አመልክተው እንደነበር የገለፁት አዘጋጆቹ፤ ከግምገማ በኋላ 60 ዘጋቢ ፊልሞች ለዕይታ መመረጣቸውን ጠቁመው “አዲስ ኢንተርናሽናል ፊልም ፌስቲቫልን” በአፍሪካ ትልቁ መድረክ ለማድረግ በአበረታች አቅጣጫ ላይ ነን ብለዋል፡፡
ከዘጋቢ ፊልሞቹ ለዕይታ መቅረብ ባሻገር ከመላው ዓለም ከመጡ የፊልም ባለሙያዎች ጋር የጥያቄ እና መልስ እንዲሁም የውይይት መድረኮች ይካሄዳሉ ተብሏል፡፡
ኢትዮጵያውያን ፊልም ሰሪዎች በፌስቲቫሉ ላይ ያላቸው ተሳትፎ አነስተኛ መሆኑን ጠቁመው ዋናው ምክንያትም ዘርፉ ብዙም ንግድ የማይሰራበት በመሆኑ ስለማያበረታታቸው ነው ብለዋል፡፡
በፌስቲቫሉ ከሚቀርቡ ዘጋቢ ፊልሞች መካከል በኢትዮጵያዊያኑ ዳይሬክተሮች ትርሲት አግዝ እና ኃይሉ ከበደ የተሰሩት “የበሬው ውለታ” እና “ትስስር” የሚገኙበት ሲሆን “35 OWS AND A KALASHINIKOV”, “5 MINUTES Of FREEDOM”, “9999”, “At 60 Km/h” የሚሉና ሌሎችም ይታያሉ ተብሏል፡፡

Published in ጥበብ

 60 ዘጋቢ ፊልሞች ለተመልካች ይቀርባሉ
  ፌስቲቫሉ በክልል ከተሞችም ይቀጥላል
      በመላው ዓለም ከተሰሩ ምርጥ ዘጋቢ ፊልሞች የተመረጡ 60ዎቹ ለዕይታ የሚቀርቡበት “9ኛው አዲስ ኢንተርናሽናል ዘጋቢ ፊልም ፌስቲቫል” ትላንት በብሄራዊ ሙዚየም የቅርስ ጥናት እና ጥበቃ ባለስልጣን አዳራሽ ተከፈተ፡፡ ፌስቲቫሉ ለአምስት ቀናት እንደሚካሄድ የገለፁት የ“ኢንሺዬቲቭ አፍሪካ” ዋና ዲያሬክተር አቶ ክቡር ገና፤ በቀጣይ ዓመታት ፌስቲቫሉ የራሱን ውድድር አድርጎ ፊልሞችና ፊልም ሰሪዎችን ለመሸለም እንዲሁም ኢትዮጵያዊያን ፊልም ሰሪዎች በዘጋቢ ፊልሞች ስራ የተሻለ ተሳትፎ እንዲኖራቸው እንተጋለን ብለዋል፡፡ ፌስቲቫሉ የተከፈተው በሩት ኢሼል ዳይሬክተርነት በተሰራው “Shoulder Dancing” የተሰኘ ዘጋቢ ፊልም ነው፡፡ እስከ ሰኔ 9 በሚዘልቀው ፌስቲቫል፤ 60 የሚደርሱ ዘጋቢ ፊልሞች ለዕይታ የሚቀርቡ ሲሆን በአዲስ አበባ  በቅርስ ጥናትና ምርምር ማዕከል፤ በሀገር ፍቅር ትንሽዋ አዳራሽ፤ በብሪትሽ ካውንስል እና በአሊያንስ ኢትዮ ፍራንሲዝ ለተመልካቾች ይታያሉ፡፡ የፊልም ፌስቲቫሉ ሰኔ 19 እና 20 ደግሞ በአዳማ፤ ባህርዳር፤ ሃዋሳ እና መቀሌ  ከተሞች እንደሚካሄድ ተገልጿል፡፡
በዘንድሮው ፌስቲቫል በዓለማችን አበይት የመነጋገሪያ አጀንዳዎች ላይ ተመርኩዘው የተሰሩ ዘጋቢ ፊልሞች ተመርጠው መቅረባቸውን በጋዜጣዊ መግለጫው የተናገሩት አቶ ክቡር ገና፤ ከ10 በላይ የፊልም ዳይሬክተሮችን ከተለያዩ አገራት በመጋበዝ በፊልሞቹ ዙሪያ ከተመልካች ለሚነሱ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጡበት መድረክ መመቻቸቱንም ገልፀዋል፡፡ ባለፈው ዓመት ከ10ሺ በላይ ታዳሚ የነበረው አዲስ ኢንተርናሽናል ዘጋቢ ፊልም ፌስቲቫል፤ ዘንድሮ ደግሞ በፊልሞቹ ብዛት፤ በሚቀርቡት ዘጋቢ ፊልም ሰሪዎች የብቃት ደረጃና አይነት እንዲሁም በሚያገኘው ተመልካች ብዛት በአፍሪካ ግዙፉ ፌስቲቫል ይሆናል ተብሎ ይገመታል፡፡ በፌስቲቫሉ ላይ ለመሳተፍከመላው ዓለም 500 ፊልሞች አመልክተው እንደነበር የገለፁት አዘጋጆቹ፤ ከግምገማ በኋላ 60 ዘጋቢ ፊልሞች ለዕይታ መመረጣቸውን ጠቁመው “አዲስ ኢንተርናሽናል ፊልም ፌስቲቫልን” በአፍሪካ ትልቁ መድረክ ለማድረግ በአበረታች አቅጣጫ ላይ ነን ብለዋል፡፡
ከዘጋቢ ፊልሞቹ ለዕይታ መቅረብ ባሻገር ከመላው ዓለም ከመጡ የፊልም ባለሙያዎች ጋር የጥያቄ እና መልስ እንዲሁም የውይይት መድረኮች ይካሄዳሉ ተብሏል፡፡
ኢትዮጵያውያን ፊልም ሰሪዎች በፌስቲቫሉ ላይ ያላቸው ተሳትፎ አነስተኛ መሆኑን ጠቁመው ዋናው ምክንያትም ዘርፉ ብዙም ንግድ የማይሰራበት በመሆኑ ስለማያበረታታቸው ነው ብለዋል፡፡
በፌስቲቫሉ ከሚቀርቡ ዘጋቢ ፊልሞች መካከል በኢትዮጵያዊያኑ ዳይሬክተሮች ትርሲት አግዝ እና ኃይሉ ከበደ የተሰሩት “የበሬው ውለታ” እና “ትስስር” የሚገኙበት ሲሆን “35 OWS AND A KALASHINIKOV”, “5 MINUTES Of FREEDOM”, “9999”, “At 60 Km/h” የሚሉና ሌሎችም ይታያሉ ተብሏል፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 13 June 2015 15:43

‹‹ማሂ ድንግሏ››

ልጃገረድነት ሰልችቶኛል፡፡ ቦይፍሬንድ አምሮኛል፡፡
‹‹የኔ ፍቅር››  መባል፣ ‹‹የኔ ቆንጆ›› ተብሎ መጠራት አሰኝቶኛል፡፡
እስከዛሬ ድረስ ‹‹ትምህርቴን በስርአት ለመከታተል››፣ ‹‹ከአልባሌ ቦታ ለመራቅ››፣ ‹‹መቅደም ያለበትን ለማስቀደም››፤ የከጀሉኝን በአልገባኝም እየሸወድኩ፣ የጠየቁኝን እምቢ እያልኩ፣ ስንት የተቀበረ የወንድ ፈንጂ በጥንቃቄ አልፌ፤ ልጃገረድ ሆኜ ቆይቻለሁ፡፡
ኮሌጅ ከገባሁ ጊዜ አንስቶ ግን ከካልኩለስ በላይ ይሄ እየከበደኝ መጣ፡፡ አብሶ ሶስተኛ አመት ስደርስ። አብሶ 21 አመት ሲሞላኝ፡፡ አብሶ ጓደኞቼ ሁሉ ወሬያቸው በ ‹‹እንትና ደውሎልኝ›› ፣ በ‹‹ እንትና ቴክስት ልኮልኝ››፣ በ‹‹እንትና ስሞኝ›› ሲጀምርና ሲያልቅ፤ እኔ ደግሞ ከወሬው መገለል ስጀምር፡፡
እኔ ስልክ የሚደውልልኝ ታላቅ ወንድሜ ብቻ ነው፡፡ ቴክስት የሚደርሰኝ ከ8100 ብቻ ነው፡፡
ተስሜ የማውቀው አስራ አንደኛ ክፍል እያለን አሳስቶ (ለአራት ወራት) በቀመሰኝ ዮናታን ብቻ ነው፡፡
እነሆ! ድንግል መሆኔን ያወቁት የቅርብ ጓደኞቼ የቀልዶች መጀመሪያ ካደረጉኝ ቆዩ፡፡
‹‹አንቺ ልጅ አረ ተይ...?! ኮርማ አምጥተን እናስጠቃሽ እንዴ..!.›› ‹‹ቱሪዝም ኮሚሽን ስላንቺ ያውቃል...? ከድንቃድንቅ ቅርሶች መሃል አስመዝግበው ያስጎብኙሽ እንጂ!››
‹‹የሆነ አራት መአዘን የመስታወት ሳጥን ውስጥ አስቀምጠው ሊመረምሩሽ እንዳይመጡ...››
ልጃገረድነት ሰልችቶኛል፡፡ ቦይፍሬንድ አምሮኛል፡፡ ‹‹የኔ ፍቅር›› መባል፣ ‹‹የኔ ቆንጆ›› ተብሎ መጠራት አሰኝቶኛል፡፡
ግን ቦይፍሬንድ እንዴት እንደሚገኝ፣ ልጃገረድነት እንዴት እንደሚሰጥ፣ የኔ ፍቅር ለመባል በየት በኩል እንደሚኬድ አጥርቼ ስለማላውቅ፣ ጓደኞቼ ሲወጡና ሲገቡ ማጥናት፣ አንዳንዴም ጥያቄ መጠየቅ፣ አንዳንዴም ዝም ብለው ሲያወሩ ከዝባዝንኬው ፍሬ ነገር መልቀም ያዝኩ፡፡
ልክ ክፍል ውስጥ ገብቼ ደብተሬ ላይ ዋና ዋናውን እንደምፅፈው፤ ከአፋቸው የሚወጡ ነገሮችን ጆሮዎቼን አፋቸው ስር እንደ ባልዲ ደቅኜ መቅዳት ጀመርኩ፡፡
ብዙ ጊዜ የሚጠቅመኝን ነገር የምታወራው ግን ሰምሃል ነበረች፡፡
ሰምሃል እንደ ኤቲኤም ማሽን ለወንዶች ሃያ አራት ሰአት ክፍት ናት፡፡ በተለይ የሚስጥር ኮድዋን ለሚያውቁ፡፡
‹‹የሴቶች ቫያግራ ገንዘብ ነው ›› የምትለው ነገር አላት፡፡ ገንዘብ ካገኘች እንደ ህዝብ ስልክ ማውራት ትጀምራለች፡፡ አውርታም የተጠየቀችውን ታደርጋለች፡፡
አንድ ቀን ዶርም ለብቻችን ስንሆን ድፍረት አጠራቀምኩና፤ ‹‹ ስሚ ሰምሃል...›› አልኳት ‹‹እ...››
‹‹እንዳትስቂ ግን›› ‹‹በምን እስቃለሁ...?›› ‹‹በምጠይቅሽ ነገር›› ‹‹ምንድነው...የሚያስቅ ነው.?..››
‹‹ኦፋ! አትሳቂ አልኩሽ አይደል..?.›› ‹‹እሺ.. ጠይቂኝ›› የእግር ጥፍሮችዋን አይን የሚያደነቁር ቀይ ቀለም እየቀባች ነው፡፡ ጎንበስ ብሎ ለሞከረ ከአውሮፕላን ይታይ ይመስለኛል፡፡
‹‹እ...ቦይፍሬንድ...ቦይፍሬንድ እንዴት ነው የሚያዘው...ማለቴ...መጀመሪያ ምን ማድረግ ነው ያለብኝ...?››
አልሳቀችም፡፡ ገረመኝ፡፡ ‹‹ማሂዬ! የኔ ቆንጆ....ልብስ እንዴት ነው የሚገዛው...?›› አለችኝ ቀለም ቅቡን ትታ ወደኔ እያየች፡፡ ‹‹እ..?››
‹‹ልብስ ስትገዢ ምንድነው የምታደርጊው...?›› ‹‹እለካለኋ!›› ‹‹እኮ...ወንድም እንደዛ ነው...ገበያ ትወጫለሽ....፣ ያማረሽን ታነሲያለሽ...ትለኪዋለሽ....ካልጠበበ...ወይ ካልሰፋ...በልክሽ የሆነውን በአቅምሽ ትገዣለሽ....››
ብዙ ጊዜ የምትለው ነገር አይጥመኝም ነበር፤ ይሄ ግን ልክ መሰለኝ፡፡
በልክ መግዛት፡፡ በአቅም መግዛት፡፡
ግን ልኬ ማነው...? አቅሜስ ምን ያህል ነው...? ወንድን ‹‹መለካት››ስ ምን ማለት ነው...? ስንት ምሳ ተጋብዤ እመርጣለሁ?
ስንት ከንፈር ቀምሼ አውቃለሁ?
ከስንቱ ጋር ተኝቼ እወስናለሁ...?
ብዙ ያልተመለሱ ጥያቄዎች ነበሩኝ ግን፤
ልጃገረድነት ሰልችቶኛል፡፡ ቦይፍሬንድ አምሮኛል፡፡
‹‹የኔ ፍቅር›› መባል፣ ‹‹የኔ ቆንጆ›› ተብሎ መጠራት አሰኝቶኛል፡፡
ስለዚህ በፈራ -ተባ ቦይፍሬንድ ገበያ ወጣሁ፡፡
ምን ያደርጋል! የምሄድበት ቦታ ሁሉ የኖህ መርከብ ይመስል ካለ ጥንድ ብቻውን የቆመ ሰው ግን አጣሁ፡፡
አልፎ አልፎ ብቻውን የቆመ ባገኝም፤ ለምሳሌ አንዱ መላጣ እና ሾጣጣ ጭንቅላታም ይሆንና ‹‹አሁን ይሄ መላጣ ሌላ ፊት አያሰራም!?›› እያልኩ ስስቅ የቦይፍሬንድ ግዢውን እረሳለሁ፡፡
እንዲህ እንዲህ እያልኩ አቃቂር ሳወጣ ውዬ ባዶ እጄን እመለሳለሁ፡፡
-----
ሙከራ አንድ!
ከእለታት በአንዱ ቀን በሰምሃል አያያዥነት ከአብስራ ጋር ተዋወቅሁ፡፡
ለነገሩ በፊትም አውቀው ነበር፡፡ ‹‹ጓደኝነታችን›› ሲጠነክር እና በግ ተራ እየተቀጣጠርን መገናኘት ስንጀምር የነገሩን አቅጣጫ በመገመት ለሚመጣው መዘጋጀት ጀመርኩ፡፡ የዚያን ጊዜ ነው ሰምሃል የአብስራም እንደኔ ‹‹ልዩና አስደናቂ ወጣት›› እንደሆነ የነገረችኝ፡፡ ጎበዝ የማትስ ዲፓርትመንት ተማሪ ስለነበር ‹‹በሂደቱ ላይ›› ችግር ቢፈጠር መላ መምታት አይከብደውም ብዬ ብዙ አልከፋኝም፡፡
ከጥቂት ሳምንታት በኋላ ተከራይቶ የሚኖርበት ቤት ወስዶ ‹‹የሚያሳብድ ሙዚቃ›› ሊያሰማኝ እንደሚፈልግ ሲነግረኝ በጠዋት ወጥቼ የውስጥ ሱሪ ገዛሁ፡፡ ቀይ፣ ባለ አበባ፣ የመቀመጫዬን  አንድ አራተኛ ብቻ የሚሸፍን “ሻፋዳ” የውስጥ ሱሪ፡፡
እንደ ጎበዝ ተማሪ ባህሪዬ፤ ከዚያ በፊት በነበሩት ቀናት ግን ሰምሃልና ሌሎቹ ባሉበት የቅድመ ዝግጅት ጥያቄዬን ልምድ ላካበቱት አቅርቤ ነበር፡፡
‹‹ያማል?›› ‹‹አዎ ግን አሪፍ ህመም ነው››
‹‹ካደረግኩ በኋላ ወዲያው መቆምና መራመድ እችላለሁ?›› (ከህብረት ሳቅ በኋላ) ‹‹እንዴ! ስልክ እንጨት የምትውጪ መሰለሽ እንዴ?!›› ሰምሃል ናት፡፡
‹‹ከሱሬ ጋር ካላደረግሽ...ቆመሽ ትሄጃለሽ...›› ሁሉም ጮህ ብለው ሳቁ፡፡ ‹‹ሱሬ ደግሞ ማነው?›› ሌላ የማላውቀው ነገር ከጣሪያ በላይ ሲያስቅ እኔ ግን መጠየቅ እየሰለቸኝ ጠየቅኩ፡፡ ‹‹ሱሬ ቲቪኤስ ነዋ! ሱሬን አታውቂውም?›› ሰምሃል ተሽቀዳድማ፡፡ ‹‹ሱሬ ማ?››
‹‹ሱሬ ቲቪኤስ!›› እንደገና ሳቁ፡፡ ‹‹ምንድነው ደሞ ቲቪኤስ?›› እያመመኝ ጠየቅኩ፡፡
ሶስቱም በአንድ ጊዜ እንዳጠኑት ሁሉ እኩል ‹‹ባለ ሶስት እግር ተሽከርካሪ!›› አሉና እንደገና ሳቁ፡፡
አፍሬም ስቄም ዝም ብዬ ትንሽ እንደቆየሁ ማክዳ ‹‹ለመጀመሪያ እንኳን ባለማርያም ጣቱን ያድርግልሽ›› አለች ከቅድሙ የተረፈ ይሆን አዲስ  ያላወቅኩትን ሳቅ ሳታቆም፡:
ስቄ ዝም አልኩ፡፡
‹‹ባይ ዘ ዌይ...ክብሩ እንደዛ ነው አሉ›› (ያው እንደምትገምቱት ሰምሃል ናት ይሄን ያለችው) ‹‹ክብሩ..? ክብሩ ሳይኮሎጂ!?›› ማክዳ ተሸቀዳድማ ጠየቀች
‹‹ያ!...ሰኒ አብራው አድራ ስትመጣ እንዴት ነበር ስላት ምን ብትለኝ ጥሩ ነው?›› ‹‹ምን አለች?››
‹‹እሱ ኮንዶም ሲያመጣ እኔ ደግሞ ማይክሮስኮፕ ይዤ መሄድ ነበረብኝ!››
እኔ የሌለሁበት ሌላ የሕብረት ሳቅ፡፡ ልጃገረድነት ሰልችቶኛል፡፡ ቦይፍሬንድ አምሮኛል፡፡
‹‹የኔ ፍቅር›› መባል፣ ‹‹የኔ ቆንጆ›› ተብሎ መጠራት አሰኝቶኛል፡፡ ከእነዚህ ልጆች ሳቅ መደመር አምሮኛል፡፡
የአብስራ፤ ከላይ ጣራዋን፣ ከታች ወለሏን በማዳበሪያ ኮርኒስ የተለበጠች፣ ከትንሽነቷ ብዛት በስፋት ልኬት ልትጠራ የማይገባት ቤቱ ይዞኝ ሄደ፡፡ ፍራሽና ቴፕ ብቻ ነው ያላት፡፡
‹‹ሙዚቃ ልንሰማ..ሃሃ...ያልተበላ ብላ!›› አልኩ በሆዴ፡፡
ፍራሹ ላይ ተጣበን ተቀመጠን፡፡
ካሁን ካሁን ወጣብኝ፣ ካሁን ካሁን ሴት አደረገኝ፣ ካሁን ካሁን --- ብዬ ስጠብቅ በላዬ ላይ ተንጠራርቶ ቴፑ ውስጥ የሆነ ሲዲ ከተተ፡፡
‹‹ግርማ ይፍራሸዋን መስማት አለብሽ...!ስሚ የምር ሙዚቃ›› አለና ጎታታ የፒያኖ ሙዚቃ ከፈተልኝ፡፡
ዝም ብዬ አየዋለሁ፡፡ በግርማ ይፍራሸዋ ም..ስ...ጥ ብሏል፡፡ በቁሙ ምስጥ ይብላውና!
---------
ሙከራ ሁለት!
ሰምሃል ያጣበሰችኝ ሚኪ እየሳመኝ ነው፡፡ ሲስም እንደ ዮናታን አይደለም፡፡ ዮናታን ሲስመኝ ምላሱን የሚያደርግበት ቦታ ጠፍቶት አፌ ውስጥ ይዘፈዝፈው ነበር፡፡ አንዳንዴ ደግሞ ጥርሴን ይልስበት ነበር፡፡ እንደዛ እንደዛ ሲደርግ ሊያስመልሰኝ ይደርስ ነበር፡፡
መሳም ለካ እንዲህ ነው!
‹‹ጎበዝ ነህ..መሳም›› አልኩት የትንፋሽ መሰብሰቢያ እረፍት ስንወስድ ፈገግ አለና ዝም አለ፡፡
‹‹እንዴት...የት ተማርከው በናትህ?›› ‹‹መሳም ስሜት እንጂ ሳይንስ የለውም...››
እንደገና መሳሳም ጀመርን፡፡ ዮናታን እግዜር ይይለት፡፡
ሲስመኝ ሲስመኝ...ሲስመኝ...ነገራችን ከሰሜን ወደ ደቡብ ቢዘልቅ ተመኘሁ፡፡
ባየው አይወርድም፡፡ ባየው አይወርድም፡፡
ከንፈሬን ሙጭጭ ብሎ ቀረ፡፡
የትራንስፖርት ወጪ ያለበት ይመስል ሰሜን ላይ ሙጭጭ አለ፡፡
አቅበጠበጠኝ፡፡ እጁን በእጄ ይዤ ወደ ደቡብ ተጓዝኩ፡፡
ዋናው ከተማ ላይ ከተመ፡፡ ጎሽ!...
በድንገት ግን ባልጠበቅኩት ፍጥነት ዋና ከተማውን ማተራመስ ጀመረ፡፡
ተናወጥኩ፡፡ ደነገጥኩ፡፡
እሱ ሲቸኩል እኔ አዘገምኩ፡፡
እሱ ሲፈላ እኔ ቀዘቀዝኩ፡፡ ‹‹ተው!›› አልኩና ሸሸሁ፡፡
‹‹ምነው....?›› ድምፁ የሱ አይመስልም (ድምፃቸውም ይቀየራል እንዴ?) ‹‹ሚኪ...ቨርጂን ነኝ...›› ‹‹አውቃለሁ...››
‹<፣እንዴት..? ...ማለት እንዴት አወቅክ?››
‹‹እነ ሃይላብ ሲያወሩ ሰምቼ ነው..ሰምሃል ነግራው...ነገረችኝ ብሎ ነገረኝ...›› ‹‹ምኑን...?>>
‹‹ያው ቨርጂን እንደሆንሽ እና ‹‹ዲስቨርጅ›› መደረግ እንደምትፈልጊ...››
ራሴ ዞረ፡፡
‹‹ዲስቨርጅ መደረግ እንደምትፈልጊ›› በሚለው አባባል ራሴ ዞረ፡፡
ልክ እንደሚፈለጥ ኮብል ስቶን፣ እንደሚፈታ ሳይመልቲኒየስ ኤኩዌዥን፣ እንደሚተረተር ቱባ ክር መታየቴ ራሴን አዞረው፡፡
የሰዎች በኔ ጉዳይ ተወያይቶ መወሰን፣ ሴራው፣ ቅንብሩ፣ ድርድሩ አዞረኝ፡፡
ሽሽት አልኩ፡፡
ራሴን ለመታረድ ያቀረብኩ ገራገር በግ የሆንኩ መስሎ ተሰማኝና ሽሽት አልኩ፡፡
‹‹ምን ሆነሻል?›› ‹‹ምንም..ሬዲ አይደለሁም...እንሂድ....››
ሙከራ ሶስት አልነበረም፡፡
ከሚኪ በኋላ የተረዳሁት ነገር ከተጨማሪ ሙከራ አቀበኝ፡፡
ልጃገረድነት ሰልችቶኛል፡፡ ቦይፍሬንድ አምሮኛል፡፡ ‹‹የኔ ፍቅር›› መባል፣ ‹‹የኔ ቆንጆ›› ተብሎ መጠራት አሰኝቶኛል፡፡
ግን፤
ይሄን ሁሉ ስሞክር የነበረው በመገፋቴ እንጂ በመፈለጌ አልነበረም፡፡ ይሄን ሁሉ ስሞክር የነበረው ተገፍትሬ እንጂ ተራምጄ አልነበረም፡፡
ይህን ሁሉ ስሞክር የነበረው በይ በይ ተብዬ እንጂ በይ በይ ብሎኝ አይደለም፡፡
ነገም ይሆን የዛሬ አመት፣ የዛሬ አምስት አመት፣ የዛሬ አስር አመት (ወይኔ ጉዴ! እዛስ ባልደረስኩ!)
ድንግልናዬን ማስወሰድ ሳይሆን መስጠት ነው የምፈልገው፡፡ ድንግልናዬን መገላገል ሳይሆን አሽሞንሙኜ መሸኘት ነው የምሻው፡፡
ድንግልናዬን ማስገርሰስ ሳይሆን መጋራት ነው የምመኘው፡፡
Top of Form
Unlike - Comment - Share
Bottom of Form

Published in ጥበብ

 በዳንኤል ዓለሙ የተዘጋጀው “ይህን ያውቁ ኖሯል?” የተሰኘ የጠቅላላ ዕውቀት መጽሐፍ ሰሞኑን በገበያ ላይ ዋለ፡፡ በአምስት ምዕራፎች የተከፋፈለው መጽሐፉ፤ የዓለም አስደናቂ ሪከርዶች፣ የፖለቲካውና የስፖርቱ ዓለም አስገራሚና አስደናቂ እውነታዎች እንዲሁም በኢትዮጵያ ታሪክ ዙሪያ የሚያጠነጥኑ መረጃዎችን ይዟል፡፡ በ224 ገጾች የተሰናዳው መጽሐፉ፤ በ50 ብር ከ70 ሳ. ለገበያ ቀርቧል፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም “ፈተናን የማሸነፍ ጥበብ”፣ “ስኬታማ የፍቅር ህይወት”፣“ገንዘብና ጭንቀት”፣ “ራስን የመለወጥ ምስጢር” እና “ይህን ያውቁ ኖሯል? ቁ.1” የሚሉ መጻህፍትን ማሳተሙን ጠቁሟል፡፡
በደራሲ ድርቡ አደራ የተጻፈው “ሌባ ሻይ” ልብ ወለድ መፅሐፍም ለንባብ የበቃው ባሳለፍነው ሣምንት ነው፡፡ በ400 ገጾች የተቀነበበው መጽሐፉ፤ በ80 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡ ጸሐፊው ቀደም ሲል “ሐምራዊት”፣ ሽንብሩት” እና “ዲና” የሚሉ መጽሐፍትን ማሳተሙ ይታወሳል፡፡
ለአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ስለ ህዋ ሳይንስ ግንዛቤ ለመስጠት ታስቦ የተዘጋጀውና “አስትሮኖሚ ለልጆች” የተሰኘው መጽሐፍም ከሳምንቱ የህትመት ትሩፋቶች አንዱ ሆኗል፡፡ በፊዚክስ የማስተርስ ድግሪ እንዳለው በጠቆመው አክመል ተማም የተሰናዳው መጽሐፉ፤ ዩኒቨርስ፣ጋላክሲዎችና ሶላር ሲስተም በሚሉ ሶስት ምዕራፎች ተከፋፍሎ የቀረበ ሲሆን በ28 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ የትምህርት ባለሙያው አክመል፤ ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ ርዕሰ ጉዳይ ለሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎችና ለሌሎች “ዩኒቨርስ” የተሰኘ መጽሐፍ አሳትሞ ማቅረቡም ታውቋል፡፡

የገጣሚ ደምሰው መርሻ በሙዚቃ የተቀናበሩ የግጥም ሥራዎች “ያልታየው ተውኔት” በሚል ርዕስ በሲዲ የተዘጋጀ ሲሆን የፊታችን ረቡዕ ከ11 ሰዓት ጀምሮ በሂልተን ሆቴል ይመረቃል፡፡
17 ግጥሞችን ታዋቂው ሙዚቀኛ ጆርጋ መስፍን ያቀናበረለት ሲሆን 1 ግጥም ደግሞ በጥላሁን ጊዮርጊስ (ፒጁ) መቀናበሩን ገጣሚው ጠቅሶ፣ኤርምያስ ዳኜ የሁሉንም ሚክሲንግ እንደሰራለት ተናግሯል፡፡
የሲዲውን ሽፋን ሰዓሊ ዳንኤል ታዬ ሰርቶልኛል ብሏል- ገጣሚው፡፡   
በሒልተን ሆቴል በሚካሄደው የግጥም ሲዲ የምረቃ ሥነሥርዓት ላይ አንጋፋው ሃያሲ አብደላ እዝራ በግጥሞቹ ላይ ሒሳዊ ዳሰሳ የሚያቀርብ ሲሆን ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፣ ገጣሚ ኤፍሬም ስዩም፣ አርቲስት ፈለቀ አበበና ሌሎችም ለታዳሚያን የግጥም ሥራዎችን ያቀርባሉ ተብሏል፡፡ ደምሰው መርሻ በተለያዩ የጥበብ መድረኮች ላይ ግጥሞቹን አዘውትሮ በማቅረብ የሚታወቅ ተወዳጅ ገጣሚ ሲሆን የ“ግጥም በጃዝ” ቡድንም አባል ነው፡፡

Saturday, 13 June 2015 15:34

የማሸነፍ አባዜ!

…ብዙ ውጣ ውረዶችን አልፌ፣ ብዙ አንስቼ ብዙ ጥዬ፣ ብዙ አዝኜ ተደስቼ ... ከተጠለልኩበት የሽንፈት ድንኳን፣ ከሱስና ከተስፋ መቁረጥ መንደር፣ የዓለምን ጨለማ ዕኩለ ሌሊቱ ላይ ሆኜ በምዳክርበት ወቅት ላይ ነው፡፡ አዎ… የዛሬ ሶስት ዓመት ለሥራ ደብረ ማርቆስ ሄጄ፣ ከከተማው ትልቅ አደባባይ ወረድ ብሎ ካሉት ሱቆች አንዱ በር ላይ ቆሜ ሰው ስጠብቅ የሰማሁት ድምጽ … ህይወት አጎናፀፈኝ ሠላም...ተስፋ…ብርሃን…ደስታ…ፍቅር ድል…አያሌ ነገሮችን  ወደ ሕይወቴ ይዞ መጥቶ ነበር፡፡
“ይ…ቅ…ር…ታ…!” ከመላዕክቶች መንግስት የተላከች የምትመስል ወጣት እንደ ወፍ ስታዜም ሰማሁዋት፡፡
“ይቅርታ…ወንድሜ!” ብላኝ ወደ ኋላ አጣምርያቸው የነበሩትን እጆቼን ስትነካቸው እንደ ሰመመን ይታወቀኝ ነበር፡፡ ቢራቢሮዎች ሲበሩ፣ አበቦች ሲወዛወዙ የሰማሁ መሰለኝ፡፡ ከዚያም የሆነ እሳት የሚተፉ የሰው ጣቶች ነኩኝ፡፡ ከደረቀው ገላ አንገቴ ብቻ ትንሽ ወደ ኋላ መዞር ተሳካለት፡፡
በፍርሃት የታጀቡ ግን የሚያበሩ አይኖች…እንደ ዋዛ ሸብ ካደረገችው ሻሽ ሥር ሾልኮ የወጣውን ሉጫ ፀጉር የተሸከመ ረዥም አንገት…ታየኝ፡፡ ፊቴ ድቅን ያለችው እማዬ መስላኝ ነበር፤ እናቴ፡፡
“እጆችህን አጣምረህ ቆመህ ስትተክዝ ስላየሁህ ነው…በእናትህ እጆችህን አላቃቸው…”
ሠምቻታለሁ፤ ግን ማላቀቅ አልቻልኩም፡፡
“አባዬና እማዬ ከተለያዩ በኋላ አባቴ ሁሌ አሁን አንተ እንደቆምከው እጆቹን ወደ ኋላ አጣምሮ፣ ቆሞ ሲተክዝና ሲያዝን እያየሁ ነው ያደግሁት…ወንድ ልጅ እንደሱ ሲቆም አልወድም” ሠምቻታለሁ…ግን …፡፡
“እጆችህን አላቃቸው በፈጠረህ…”
አልቻልኩም… ፡፡
እሷ ዞራ ባታላቅቃቸው ኖሮ፣ እጆቼ እስከ ዛሬ እንደተጣመሩ ይቀሩ ነበር፡፡ እኔም ደብረማርቆስ አደባባይ ሥር ደርቄ ቀርቼ ነበር፡፡
 ነፍስ…ዘራችብኝ፡፡
“ወንድ ልጅ አንገቱን አይደፋም! አይዞህ! እሺ?”
“እሺ” አልኳት፡፡
ፈገግ አለች፡፡ የእማዬ ጓሮ የቡና አበባዎች ትዝ አሉኝ፡፡ እንደ ቡና አበባ የፈኩ ጥርሶች፡፡ ይህች ልጅ…ከእናቴ ጋር ምን አላት?
ማርቲን በዚህ ሁኔታ ነበር የተዋወቅኋት፡፡
ማርቲ ሚሊዮን ጥሩ ነገሮች አሏት፡፡ እሷን የምወድበት ሚሊዮን ምክንያቶች አሉኝ ማለት ነው። ሚሊዮን መልካም ነገሮች ያሏትን ልጅ ማን ነው የማይወደው?
ማርቲ እንደ “ፍቅር እስከ መቃብር”ዋ ሰብለወንጌል ናት…ንፁህ ጨዋና አፍቃሪ ናት። አትዋሽም አትደብቅም…እንደ ህጻን ልጅ ትጠነቀቅልኛለች…እንደ እናቴ ትሳሳልኛለች፡፡
ማርቲን የምወድበት ሚሊዮን ምክንያቶች አሉኝ…ነገር ግን አንዲት ኢምንት የሆነች እንከን አላት፤ እኔ የማልወድላት፡፡ ግን አንድ እና ሚሊዮን እንዴት ይነጻፀራል? አንድ ሆና ብቻዋን ከሚሊዮን በተቃራኒ የቆመች ደንቃራ አለቻት፡፡ ማርቲ ካላሸነፈች መኖር አትችልም፡፡ እንዴት ሁሌ ማሸነፍ ይቻላል?
የማርቲ የህልውና መሰረት ማሸነፍ ብቻ ነው። የማታሸንፍ ከመሰላት አትገጥምም፤ የተሸነፈች ከመሰላት ደግሞ ያንን ሁኔታ ለመቀልበስ የማትምሰው ጉድጓድ የለም፡፡  
በአንድ የተረገመ ቀን በጣም የምወደው ጓደኛዬ ለሥራ የሚሆን ገንዘብ እንዳበድረው አበክሮ ተማፀነኝ፡፡ ፍቅረኛዬ እንደመሆንዋ የሁለታችን የሆነውን ነገር ግን ለብቻዬ ሠርቼ ያጠራቀምኩትን ገንዘብ “ላበድረው ወይስ አላበድረው?” እያልኩ ከራሴ ጋር ተወዛገብኩ፡፡
ጉዳዩን ለማርቲ ባማክራትና አይቻልም ብትለኝ፣ ገንዘቡን ለባልንጀራዬ ማበደር የማይታሰብ ሊሆን ነው፡፡ ይህ ደግሞ ከምወደው ጓደኛዬ ጋር ያቀያይመኛል፡፡ ስለዚህ ማርቲ ሳታውቅ “ቶሎ እመልሳለሁ” የሚለውን የሕይወት ዘመን ባልንጀራዬን ቃል አምኜ፣ ገንዘባችንን አንስቼ ለጓደኛዬ አበደርኩት፡፡ ቶሎ … ማለት መቼ ይሆን?
ሳምንት…ወር…መንፈቅ…ዓመት…?
ባልንጀራዬ ግን ገንዘቡን እንደሰጠሁት ቶሎ በሚለው ቃል ምትክ…የቤት መኪናውን ከነሙሉ ውክልናው በሬ ላይ አቁሞት ወዳልነገረኝ መንገድ ሄደ፡፡
ማርቲ አበደች! እሷ ሠርግ ይደገስ ስትል፣ እኔ የቤት መኪና እንግዛ ብያት ሳንግባባ ቀርተን ስለነበር ግጥምጥሞሹ እሳት አቀጣጠለ፡፡ መኪናውን የገዛሁ ነበር የመሰላት፡፡ ምን ብዬ ልንገራት? ነገሮቹ ሁሉ በእኔ ከሃዲነትና እምቢ ባይነት ተደመደሙ። እሷ ካመረረች ቤተሰብ፣ ጓደኛ፣ ካህን … ማንም አይመልሳትም፡፡ ይህን እያወቅሁ በፈፀምኩት ስህተት ጥላኝ ሄደች…ወደ ጨለማዬ መልሳኝ፡፡
አርባዎቹን ያለፈ ወንድ የማይችላቸው ነገሮች ብዙ ናቸው፡፡ ዋናው ማልቀስ ይመስለኛል። ሁለተኛው አምባጓሮ፡፡ ሶስተኛው መለመን፡፡ እኔ ግን ሁሉንም ቻልኩበት…በተለይ ማልቀስና መለመኑን፡፡ የእሷን ልብ ግን ማራራት አልቻልኩም። ጭራሽ ቤቷን ቀየረች፤ ስልኳን ጠረቀመች…የፌስ ቡክ ገጿን ዘጋች…ኢ-ሜይል አትመልስም፡፡ እምጥ ትግባ ስምጥ የሚያውቅ ጠፋ፡፡ ስሟንና መልኳን ጭምር የቀየረች ሁሉ መስሎኝ ነበር፡፡
የኔ ፀሐይና የኔ ጨረቃ ላይመለሱ የጠለቁ በመሠለኝ ጨለማ ውስጥ ያላሰብኩት ነገር ተከሰተ፡፡
ይህችን ጦሰኛ መኪና እየነዳሁ ሳለ፣ ቃሊቲ ከመንገድ ትራንስፖርት መሥሪያ ቤት ዝቅ ብሎ የዋናው አስፋልት ዳር ይዛ ስትራመድ የነበረችው ሃና፤ የኔ መኪና ውሃ እንዳይረጭባት ፈርታ ስትጠነቀቅ፣ የመንገዱ ጠርዝ አንሸራቷት አንድ እግሯ ዝቅ ብሎ ካለው ጭቃ ውስጥ ገብቶ፣ ከፍ ካለው ደረቅ ቦታ በቆመችበት፣ በሌላኛው እግሯ ሚዟኗን ለመጠበቅ ስትውተረተርና ቦርሳዋን ጥላ በፍርሃት ስትወራጭ አየኋት…
በዚያች ቅጽበት ከመኪናው ዘሎ ወርዶ፣ እሷን ጐትቶ ከጭቃ ውስጥ የሚያወጣ ሰው መንገድ ዘጋ ይባላል? ከኋላዬ የነበረው የከባድ መኪና ጡሩንባ የምሬት ነበር፡፡ በኔ በኩል የነበረውን ረዳት፤ “እናንተ ቦሌ መንገድ ላይ ስለማታሽከረክሩ ለሀገር መሪ ቆማችሁ አታውቁም አይፈረድባችሁም!” አልኩትና ዳር ወጣሁለት፡፡ የሀናን ቦርሳ ማንሳት አለብኝ…መኪና ውስጥ አስገብቼ ላስቀምጣት ይገባኛል…ጭቃ የነካ እግሯንና ጫማዋን ማጠብ አለብኝ…ብዙ ሥራ ነበረብኝ፡፡
ረዳቱ እያሾፈ፤ “የየት ሀገር መሪ ናት?” አለኝ፡፡
“የነፍሴ መሪ” ስል ኮስተር ብዬ መለስኩለት፡፡
“ሕይወት ይቀጥላል…” የሚለውን አባባል መጀመሪያ የተናገረው ማን ይሆን?
ከማርታ ጋር ስንተዋወቅ የሚነገር ታሪክ አልነበረኝም፡፡
ቢኖር እንኳን ለማርታ ሰብዕና፣ ለእሷ ንፁህ ሕይወት የሚመጥን ታሪክ አልነበረኝምና…ምንም አልነገርኳትም፡፡
ለሀና ግን በየቀኑ የሚነገር የማርታ ታሪክ ነበረኝ። እሷም ሆንብላ እየነካካች ታስቀባጥረኛለች፡፡ እኔም ማውራቴን አላቆምም ግን ሁሌም መቋጫዋ አንድ ነው፡፡ “አሁን የኔ ነህ፤ ማንም ወንድ አስፋልት ዳር ላይ የማያውቃትን ሴት ጭቃ እግር አያጥብላትም፤ ካንተ በስተቀር፤ አንተ ደግሞ የኔ የሀና ፍቅረኛ ነህ፡፡”
አራት ነጥብ!!
*   *   *
አንድ እሁድ ተሲያት በኋላ በዚህችው ጦሰኛ መኪና ሰው ቀጥሮን ወደ ቄራ እየሄድን ነበር፡፡ መሃል ላይ “ዛሬ እኮ ማርታን አየሁዋት” አለችኝ ሃና ድንገት፡፡
ክው ብዬ ደነገጥኩኝ፡፡  ግን ምን አስደነገጠኝ?
“ታውቂያታለሽ እንዴ?”
“አዎን!”
“እንዴት?”
“ዝርዝሩ ምን ያደርግልሃል………?”
“ያደርግልኛል”
“በእኔ ቦታ ያለች ማንኛዋም ሴት ማርታን ለማወቅ የማትፈነቅለው ድንጋይ አይኖርም…”
“ለምን?”
“ትፈራታለህ……ስሟ ያስፈራሀል…….. ኧረ መንፈሷ ሁሉ …. እሷንማ ማወቅ ነበረብኝ”
ቄራ ብሎም ካፌ ደርሰን በረንዳው ላይ ተቀመጥን፡፡
“የቱ ጋ ነበር ያየሻት?”
“ቦሌ….ኖክ ያለውን ዜብራ ስታቋርጥ……”
“አየችን…?”
“ዜብራውን ስታቋርጥ በድንዋ ነበር የሚራመደው፤ አይታሃለች…”
ሃናን ትኩር ብዬ አየሁዋት…….የሆነ ነገር ልትናገር አፏ ላይ ነበር፡፡
“ምንድነው? ሃኒ…” አልኳት፡፡
“ምላሴን አወጣሁባት” አለችኝ፡፡
ክው አልኩኝ… ጭንቅላቴን የተመታሁ ያህል አዞረኝ፡፡
“ምነው! ምነው ሃኒ….ምን አደረኩሽ በእናትሽ…?”
“ሶሪ ጌታዬ…ዊርድ ነገር ነው ያደረኩት….አም ሪሊ ሶሪ…….”
“አይይይ ሃኒ…….ማርታን አታውቃያትም ማለት ነው”
“ምን ለማለት ፈልገህ ነው?” አፈጠጠችብኝ፡፡
“ኡ.. ፍ.. ፍ.. ፍ.. ፍ.. ፍ…” በረዥሙ ተነፈስኩኝ።
“ትፈራታለህ አይደል?” ሃና ጠየቀችኝ፡፡
“እኔ’ጃ ስሜቱ…..በቃላት አይገለጽም”
ሃናን ከፋት…ሃና ምስኪን ናት፡፡
ከወራት ስቃይ በኋላ እስዋን ያገኘኋት ዕለት ነበር ጥሩ እንቅልፍ የወሰደኝ፡፡ እሷን ማጣት አልፈልግም። ፈራኋት፡፡ እንደዚያ ሲከፋት አይቻት አላውቅም። የሃናን ፊት ለመሸሽ ስሞክር አንድ ላዳ ታክሲ ወደ ካፌው በረንዳ ተጠግቶ ሲቆም ተመለከትኩ፡፡ ከቆመው ታክሲ ውስጥም አንዲት ሴት ስትወርድ እኔና ሃና እኩል አየናት፡፡
ገባኦን ላይ እያሱ ጠላቶቹን እየተዋጋ ሲመሽበት፣ አምላኩን ለምኖ ፀሐይ ቆማለት ነበር…ይህንን ታሪክ አንድ ሰባኪ “ፀሐይ ሳትሆን ምድር ናት የቆመችው” ያለው ትዝ አለኝ፡፡ ቄራ ብሎም ካፌ አካባቢ ምድር ቆማ ነበር፡፡
የኔ ልብ ቆሟል…የሃና ቁጣ ቆሟል….የማርታ አይን እሳት ይረጫል… ያለቀሰች ትመስላለች፡፡ ቀጥ ብላ እኛ ወደተቀመጥንበት መጣች፡፡ ሲቃ ነገር ያዳመጥኩ ይመስለኛል….ፊቷን ደግሜ አላየሁትም…ትንፍሽ አላልኩም…አልተንቀሳቀስኩም፡፡ በንዴት የጦፈች ሴት፣ በሲቃ የታፈነ ድምጽ ግን ሰምቻለሁ። እሱም በቀረው ዘመኔ ሁሉ የማልረሳው የማርታ ድምጽ ነበር፡፡
“አ ባ ቢ…የመኪናውን ቁልፍ ስጠኝኝኝኝ…” ያኔ ያለቀሠች ይመስለኛል……ከመቀመጫዬ ሳልንቀሳቀስ፣ ከበድን አካሌ ላይ ደርቆ የነበረውን ቁልፍ የያዘውን እጄን ሙሴ በበትሩ ደገፈው መሠለኝ…ወደ ማርታ ተዘረጋላት…..ወሰደችው፡፡
ፊቷን የማይበት አቅም አልነበረኝም…ግን አይኖቿ ላይ የእንባ ዘለላዎች ስለመኖራቸው እርግጠኛ ነኝ፡፡
ማርታ ሙሉ ክብ ዞራ የመኪናዋን አፍንጫ ወደ መስቀለኛው ስታንቀሳቅሰው ምድር ተንቀሳቀሰች። የሰዎችና የመኪኖች ድምጽ መሰማት ተጀመረ፡፡ ማርታ እንዲህ ናት፡፡
…ካላሸነፈች መኖር አትችልም!!
የማሸነፍ አባዜ ተጠናውቷታል፡፡
ሃናም ተነስታ እየተጣደፈች ማርታ የመጣችበት ታክሲ ውስጥ ገባች፡፡ ሁሉም ካላሸነፉ መኖር አይችሉም እንዴ……….?

Published in ጥበብ
Page 8 of 16