Saturday, 27 June 2015 09:40

የፍቅር ጥግ

• ባል የቤተሰቡ ራስ ሲሆን ሚስት ደግሞ
ራስን የሚያሽከረክረው አንገት ናት፡፡
ያልታወቀ ፀሐፊ
• ራስሽን ከመሆን የሚያደናቅፍ ግንኙነትን
አሜን ብለሽ አትቀበይ፡፡
ኦፕራ ዊንፍሬይ
• ወንዶች ሴቶችን የሚያገቡት ጨርሶ
አይለወጡም በሚል ተስፋ ነው፡፡ ሴቶች
ወንዶችን የሚያገቡት ይለወጣሉ በሚል
ተስፋ ነው፡፡ ሁለቱም ግን ማዘናቸው
አይቀርም፡፡
አልበርት አነስታይን
• በካሜራ ፊት ለበርካታ ጊዜያት ባልና ሚስት
ሆናችሁ ከተጫወታችሁ በኋላ ከካሜራ
ውጭ ባልና ሚስት ቀላል ነው፡፡
ኤሚ ያስቤክ
• ትዳር ወንድ ልጅ ሚስቱ እንደምትፈልገው
እንዲያደርግ ከሚፈቅዱ ጥቂት ተቋማት
አንዱ ነው፡፡
ሚልተን በርሌ
• ግሩም ትዳር የሚባለው እንከን የለሽ ጥንዶች
ሲገናኙ አይደለም፤ ፍፁም ያልሆኑ ጥንዶች
ከእነልዩነታቸው መኖርን ሲያጣጥሙ ነው፡፡
ዴቭ ሜዩሬር
• እውነታህ ከህልምህ የተሻለ ሆኖ እንቅልፍ
መተኛት ሲያቅትህ፣ ያኔ ፍቅር እንደያዘህ
ትገነዘባለህ፡፡
ዶ/ር ሴዩስ
• በትዳር ውስጥ ደስታን ማግኘት ሙሉ
በሙሉ የዕድል ጉዳይ ነው፡፡
Pride & Prejudice
• ሚስትህ እንድታዳምጥህ ከፈለግህ ከሌላ
ሴት ጋር አውራ፡፡ ያኔ ሁሉነገሯ ጆሮ
ይሆናል፡፡
ሲግመንድ ፍሩድ
• ቦርሳዬን ስመለከት ባዶ ሆነብኝ፡፡ ኪሶቼንም
ብፈትሽ ባዶ ሆኑብኝ፡፡ ልቤን ስመለከት ግን
አንቺን አገኘሁሽ፡፡ ያን ጊዜ ነበር ሃብታም
መሆኔን የተገነዘብኩት፡፡
ያልታወቀ ፀሐፊ
• ፍቅር አ ንድ ረ ዥም ጣ ፋጭ ህ ልም ሲ ሆን
ትዳር ከእንቅልፍ የመቀስቀሻ ደወል ነው፡፡
ምንጩ ያልታወቀ
• ስኬታማ ወንድ የሚባለው ሚስቱ ማጥፋት
ከምትችለው በላይ ገንዘብ የሚሰራ ሲሆን
ስኬታማ ሴት እንደዚያ ዓይነቱን ወንድ
ማግኘት የቻለች ናት፡፡
ላና ተርነር
• ትዳር ልክ ወደ ጦርነት እንደመሄድ ያለ
ጀብዱ ነው፡፡
ጂ. ኬ. ቼስቴርቶን
• ፍቅር፤ በትዳር ሊድን የሚችል ጊዜያዊ
እብደት ነው፡፡
አምብሮሴ ቢርስ
• ለደስተኛ የትዳር ህይወት ወንዶች ሁለት
ነገሮችን ልብ ማለት አለባቸው፡- ሲያጠፉ
በፍጥነት መናዘዝን ፣ ትክክል ሲሆኑ ዝም

Published in ጥበብ

ወጣት ገጣምያን ሰቆቃ ላይ ማተኮራቸው አሳስቦታል

   ከአንድ ሳምንት በፊት ረቡዕ ምሽት ነበር ገጣሚ ደምሰው መርሻ “ያልታየው ተውኔት” የተሰኘውን በሙዚቃ የተቀናበረ የግጥም ሲዲ በሒልተን ሆቴል ያስመረቀው፡፡ በግጥም ሲዲዎች ምረቃ ላይ ባልተለመደ መልኩ ሥራዎቹን በአንጋፋው የሥነ ፅሁፍ ሐያሲ በአብደላ እዝራም አስተንትኗል። ሃያሲው ወደ ትንተናው ከመግባቱ በፊትም የሚከተለውን መንደርደርያ አስቀድሟል፡፡  
*   *   *
ደምሰው መርሻን የመተዋወቅ ዕድል ያገኘሁት በጓደኛዬ በአለማየሁ ገላጋይ በኩል የዛሬ ሁለት ዓመት ነበር፡፡ ያን ጊዜ አንብቤው ከሁለት ዓመት በኋላም ያልረሳሁት ብቻ ሳይሆን በቃሌ የያዝኩት አንድ የደምሰው ግጥም አለ፡፡ “የደሀ እናት ተስፋ” ይላል ርዕሱ፡፡ የደሀ እናት ተስፋዋ ለሚካኤል፣ ለማርያም መሳል አሊያም ፈጣሪዋን በፀሎት መለመን እንደሚሆን ነው  የምንገምተው። የደምሰው መርሻ ግጥም ላይ ያለችው እናት ግን አንድን ትንቢት ተከትላ ነው ተስፋ ያደረገችው፡፡
ካንዲት ደሀ እናት
ይወለዳል ንጉሥ
ይወለዳል ጀግና
መባሉን ሰምቼ
አምና ጀግና ወለድኩ
ርሀብ እየላሰኝ
ችግር ላይ ተኝቼ፡፡
እነሆ ዘንድሮም አረገዝኩ
ያለመጠራጠር ንጉሥ እንደሚሆን
በእምነቴ ፀንቼ፡፡
ይህን ግጥም ከሰማሁ በኋላ ልቤን ስለሰረሰረው ሒሳዊ ንባብ ጽፌበት ነበር፤ ዛሬ በሚመረቀው ሲዲ ውስጥም ታትሟል፡፡ ግጥም ሲነበብና ግጥም ሲደመጥ ልዩነት አለው፡፡ ሙዚቃ ያጀበው ግጥም ሌጣውን ሲቀርብ ግጥም ሆኖ ከተነበበ ጠንካራ ነው። ግጥሙ ያለሙዚቃ ሲነበብ ከፈዘዘ፣ ሙዚቃው ይሆናል ነፍስና ሕይወት የዘራበት፡፡ ግጥም በጃዝ ሙዚቃ ማቅረብ በአማርኛ የሥነ ግጥም ታሪክ አዲስ ነው፡፡ በዚህ መሰል መድረክ ለመሳተፍ ሰዎች ከተለያየ ጫፍ መጥተው መሰባሰባቸውም ድንቅ እርምጃ ነው፡፡
እንዲህም ሆኖ ለጥናትና ምርምር የሚጋብዙ ጥያቄዎች መነሳታቸው አይቀርም፡፡ በጃዝ ሙዚቃ ታጅቦ ከሚቀርበው ግጥም የምንሰማው ሙዚቃውን ነው ወይስ ግጥሙን? ከአዳራሽ ከወጣን በኋላ አዕምሯችን ላይ የሚቀሩ ስንኞች አሉ? የግጥሙ እሳቦትስ በውስጣችን ይሰርፃል? ምንስ ትዝታ ይቀርልናል? አመጣጣችንስ ከእነ እከሌ ጋር ነበር ለማለት ነው ወይስ ግጥም አድናቂ ሆነን ነው የምንመጣው? አነጋጋሪ ጥያቄዎቹ እንዳሉ ሆነውም ግጥም በጃዝ በመጀመሩ ለአማርኛ ሥነ ግጥም ዕድገት አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡
ለመግቢያ ያህል ይህን ካልኩ ዛሬ ወደሚመረቀው ሲዲ እንምጣ፡፡ ለግጥም ስብስቦቹ “ያልታየው ተውኔት” የሚለው የሲዲ ርዕስ የሚመጥነው አይደለም፡፡ ያንስበታል፡፡ አንድ ሰው ሲዲውን ታክሲ ውስጥ ጥሎት ቢወጣ፣ የሚያገኙት ሰዎች ርዕሱን አይተው ሊሉ የሚችሉት፤ “አዲስ የወጣ ፊልም ወይም ቴአትር” ነው፡፡
ይህ ርዕስ ለሲዲው በርዕስነት ለምን ተመረጠ ብለን ብንገምት፣ ከምናገኘው መልስ አንዱ በጃዝ በታጀበ የግጥም ንባብ መድረክ ብዙ ጭብጨባ ያገኘ ስለሆነ ይሆናል፡፡ በብዙ መድረኮች እንደሚታየው፣ በሚነበበው ግጥም ውስጥ ፖለቲካዊ ጉዳይ ከተነሳ ጭብጨባው ይደምቃል፡፡ የሱቅና የቤት ኪራይ ያስጨነቀው፣ በፍርሀትና ስጋት ውስጥ ያለ፣ በመንገድ ትራንስፖርት ችግር መከራውን እየበላ ያለ ሰው ርዕሰ ጉዳያቸውን ፖለቲካ ላደረጉ ግጥሞች በጭብጨባ ድጋፍ ይሰጣል፡፡
ርዕሱ ለሲዲው ባይመጥነውም የሽፋን ስዕሉ ግን ውብ ነው፡፡ በሲዲው በስተቀኝ በኩል ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን ፒጃማ ለብሰው፤ ከቤታቸው በርግገው የወጡ ዓይነት ሰው ሆነው ይታያሉ፡፡ ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን “እኔ ለእኔ ኖሬ አላውቅም” የምትል ኃይለኛ ግጥም አላቸው፡፡ ስዕሏ ለተመልካች ብዙ ነገር የምታስታውስ ናት፡፡
“ያልታየው ተውኔት” ከማለት ይልቅ ለሲዲው በርዕስነት ሊመጥኑ የሚችሉና ጠንካራ መልዕክት ያላቸው የግጥም ርዕሶች ነበሩ፡፡ ለምሳሌ “ያሞራ አዳኝ ሚስት” የሚለው ግጥም ርዕስ እኔን ስቦኛል። ይህች ሴት የዝሆን፣ የአንበሳ፣ የጠላት አዳኝ ሚስት ብትባል የሚያኮራ ጉዳይ ነው፡፡ አሞራ ለማደን ጫካ የሚገባ ጀግና ያለ አይመስለኝም፡፡
ደምሰው መርሻ ግጥሙን በደንብ ይጽፍና ማወሳሰብና ማውጠንጠን ሲጀምር ባልታወቀ ምክንያት ይጠመዘዝና ፖለቲካ ውስጥ ይገባል፡፡ ከዚያ በኋላ ነገሩ ይፈራርሳል እንጂ እንደጀመረው ቢቀጥል የፖለቲካውን ጉዳይ አንባቢያን መጨመር ይችሉ ነበር፡፡
“ያልታየው ተውኔት” ውስጥ እነዚህ ድንቅ ስንኞች ቀርበዋል፡ -
ደንታ ቢስ አዘጋጅ ተመልካች የናቀ
ምንም አልከበደው እያለ ሲናገር
ቴአትር አለቀ፤
የዋሁ ተመልካች ለመጠየቅ ፈርቶ
ስንት ጊዜ ወጣ መጋረጃ አይቶ
ሕዝብ ያሳዝናል
ተስፋ ብቻ ሳይሆን
ወሬም ይርበዋል፡፡
እንዲህ ዓይነት ጥልቀት ያለው ግጥም መጨረሻው ላይ ወደ ፖለቲካው ዘው ብሎ ባይገባ ኖሮ እንደ ባለቅኔ ሥራ ዘመን የሚሻገር ሊሆን ይችል ነበር፡፡ “ያ ትውልድ” በመባል የሚታወቁት የ1960ዎቹ ገጣሚያን፣ ከዚያ ዘመን ሥራዎቻቸው ወደ ዛሬ ዘልቀው የምናስታውሳቸውና ዘመን ተሻጋሪ መሆን የቻሉት ቅኔያዊ የሆኑት የዮሐንስ አድማሱና መሰል ገጣሚያን ሥራዎች ናቸው፡፡ የጠወለጉት ግጥሞች ዘመን ያለመሻገራቸው ምክንያቱ ዘገባዊ ስለነበሩ ነው፡፡
ሆረስ የሚባል ፈላስፋ ብዙ አስተውሎ የፃፈው አንድ ነጥብ አለ፡- “ንፁሕ ውሃ ብቻ የሚጠጣ ባለቅኔ የተለየ ግጥም ሊፈጥር አይችልም፡፡ ንፁሕ ውሃ ብቻ የሚጠጡ ገጣሚያን ሥራዎች ለረዥም ጊዜ የሚመስጡ ወይም የዘመን ቃፊሩን የሚሻገሩ አይደሉም” ይላል፡፡ የዚህ መዕልክት ዋነኛ አንደምታ፤ ባለቅኔ ወይም ገጣሚ ተራ ሕይወት መኖር የለበትም፤ተገልሎ ሊኖርም አይገባም፡፡ ጉራንጉሩን፣ የውስጥ ሕይወትን፣ የሰውን ልብ ትርታ ተከትሎ ካልፃፈ በስተቀር ባለቅኔ አይሆንም የሚል ይመስለኛል፡፡ የ4 ትውልዶች ታሪክ የተቀበረበት መንደር በሆነው በካዛንችስ የተወለደው ደምሰው መርሻ፤ ከ18 የሲዲ ግጥሞቹ ሁለቱ ብቻ ናቸው በወንድና በሴት ፍቅር ዙሪያ ያጠነጠኑት፡፡ ይህ ብዙ ጥያቄን ሊያስነሳ የሚችል ነው፡፡
የካዛንችስ ልጅ ሆኖ ሕይወቱ ከፍቅር ይልቅ በፖለቲካው ለመነካት እንዴት ቻለ? በፍልስፍናና በመጽሐፍ ቅዱስ ጥቁምታዎች ላይ ትኩረቱን ያበዛበት ምክንያት ምንድነው? ሳያፈቅር፣ በሴት ሳይፈቀር፣ በፍቅር ሳይንገላታ አልፏል ወይ? ያሰኛል። ከፍቅር ነክ ግጥሙ አንዱ “ናፍቆት” የሚል ርዕስ አለው፡፡ በጣም የሚገርመው ግን በዚህም ግጥሙ፣ ፍቅረኛው ስለናፈቀችውና ስለወደዳት እንድትመጣ አይፈልግም፡፡
ብጓጓ ነው የኔ ዓለም
ዓይንሽ ቢርበኝ ነው ሕመሜ
አቅም ማጣቴ እሱ ነው
ናፍቆት ነው የጣለኝ ውዴ
የሞቱ ነፍሳት
በምን እንደሞትኩ ሲያስጠይቁኝ
አፌን ሞልቼ የምናገረው
የድፍረቴ ቃሌ
እንዳይበላሽ ናፍቆት ነው እንድል
አትምጪ የኔ ዓለም አልይሽ ፍቅሬ።
ይህንን ግጥም አድምጠን ስለ ፍቅር ገጠመ ልንል አንችልም፡፡ ነፍሱን ይማረውና የደበበ ሰይፉ ግጥም ትዝ ይለኛል፡፡ “ተይው እንተወው” የሚል ርዕስ ያለው ግጥም ጽፎ ነበር፡፡ ግጥም የፃፈላት ሴትና እሱም ኃይለኛ ፍቅር ላይ ወድቀው ፍቅራቸውን ለአጭር ጊዜ ካጣጣሙ በኋላ በሆነ ፖለቲካዊ ወይም ማሕበራዊ ጉዳይ አብረው መዝለቅ ባለመቻላቸው ነበር ግጥሙን የፃፈው፡፡
የዘመን ቃፊሩን ማለፍ አልቻልና
የዓለም ጥበቱ አልመጠነና
ተይው እንተወው
ውጥኑ ግብ ይሁን ጅማሬው ፍፃሜ
ቅጽበቷ ሙሉ ዕድሜሽ ወቅቷ ዘላለሜ፡፡
ደምሰው መርሻ በአብዛኛው ኮስተር ያሉ ጉዳዮች ላይ ነው የፃፈው፡፡ 6 ያህል ግጥሞቹ ከመጽሐፍ ቅዱስ ጥቁምታዎች የወጡ ሲሆኑ ከእነዚህም መካከል፡- “ደመራና መስቀል”፣ “የጠንቋይ ቤት እውቀት”፣ “ፈጣሪና ፍጡር”፣ “መምህር ሆይ ስማኝ”፣ “ቃየልና ኦሪት”፣ “የክርስቶስ ሐሙስ” ተጠቃሽ ናቸው። ደምሰው መጽሐፍ ቅዱስን በጥሞና ያነበበ ሰው ነው፡፡ ይህንን ያደረገው ዲያቆን ለመሆን ወይም የቤተክርስቲያን ሹመት ለማግኘት አይደለም። እኛ የምናውቀው ደመራና እሱ የገጠመው ደመራ ይለያያል፡፡ ብዙዎቻችን ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ስለምናውቅ የግጥሞቹ መልዕክት በቀላሉ ይገባናል እንጂ የአዕምሯችንን ስፋት ሊያበለጽገው አይችልም።
ደምሰው መርሻ ዘመናዊ ፍልስፍና፣ ኤግዚስተንሻሊዝም፣ አብሰርዲቲ ወይም የሊቃውንት ታሪክ -- ቢቀር ቢቀር ደግሞ የአማርኛ ልቦለዶችን ቢያነብ አዳም ረታ በ “መረቅ” ልቦለድ መጽሐፉ ሰብለወንጌል መሸሻን ሕይወት ዘርቶባት፣ ትዳር መሥርታ፣ ልጅ ወልዳ እንዳሳየን፣ ድልና ጀግንነትን ይተርክልን ነበር፡፡ ራስን በመጽሐፍ ቅዱስ እውቀት ብቻ መቀንበብ ከዘመኑ ጋር ሊያስኬድ አይችልም። ወጣት ገጣሚያን የንባብ አድማሳቸውን አስፍተው ሳይኮሎጂ፣ ሶሲዮሎጂ…በስፋት ማንበብ ይኖርባቸዋል፡፡
የደምስ ግጥሞች ለጭቁኖች የሚያደሉት፤ ገጣሚው ለተጐሳቆሉ ልቡን ስለሰጠ፣ የካዛንችስ የጓዳ ገመና ልቡን ስለላጠው ሊሆን ይችላል፤ ጨለምተኞች ናቸው፡፡ መሸነፍ በውስጣቸው አለ፡፡ ብሶት ቢኖር፣ በደል ቢኖር፣ ሰው ያምፃል፡፡ መሣሪያ ያነግባል፡፡ ብዕሩን ይስላል፡፡ እንጂ እጆቹን ብቻ አጣምሮ መቀመጥ ይከብዳል፡፡
ማርክስ ትራንድ የሚባል ታዋቂ አሜሪካዊ ገጣሚ ስለ ሀዘን የፃፉ ሰዎች በዙበትና፤ “የስቃይ አረቄ በግጥም ሲወጣ፣ ብሶትም ዳግም አረቄ ሲሆን፣ በመጨረሻ ስቃዩ ሲያበቃ ደስታ ይሆናል” ብሏል፡፡ ወጣቶች እየተነሱ ስለ ሰቆቃ ብቻ የሚጽፉ ከሆነ፣ ማነው ስለ ደስታ መፃፍ ያለበት? በደሃው ቤት፣ የኩራዝ ጭላንጭል በሚታይበት ቤት--- ደስታ አለ፡፡ መፍካት አለ፡፡ ሽሮ እየበላ፣ ቆሎ እየቆረጠመ፣ ወዝና ደም ግባት ያለው ትውልድ አለ፡፡ ይህ እውነትና ተስፋ ሊጋረድብን አይገባም፡፡ ስለ ስቃይ ብቻ በምንገጥምበት ወቅት የስቃይ ሱስ የያዘን ይመስላል። ይህ ካልሆነ ሁሉንም ነገር በሚዛናዊነትና በእኩል ሁኔታ ማቅረብ ተገቢ ይሆናል፡፡
ለማጠቃለል እናቶቻችን ሽንኩርት ሲከትፉ የላይና የታቹን እየቆረጡ በመጣል መሐሉን እንደሚጠቀሙበት ሁሉ የደምሰው መርሻ ግጥሞችም ፖለቲካዊ ይዘት ያላቸውንና መሰል አላስፈላጊ ጉዳዮችን እየጣልን ካነበብናቸው (ካደመጥናቸው)፣ ዘመን ተሻጋሪ ሥራዎች እንዳሉት እንረዳለን፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 27 June 2015 09:37

‹‹እንዲያው ለጨዋታ››

--ያ ግሪካዊ መንፈስ፤ ከዚያ ጀምሮ እስከ ዛሬ ሞቶ እንደ ተቀበረ ቀርቷል፡፡ ‹‹በነገርህ ሁሉ ምጥን ሁን›› የሚል ወርቃማ ህጓን የተወችው ግሪክ፤ ብድር አብዝታ ወስዳ በማጣጣር ላይ ትገኛለች፡፡ ከእነ አቴና ወይም ስፓርታ ጋር ስትነፃፀር ትልቅ ግዛት ያላት ቢሆንም፤ ትንሽ ሐገር ነች፡፡---

‹‹ዘመናዊው የዓለማችን ሰው በጠቅላላ፤ ‹ትልቁ› የሚል ቃል ይወዳል›› የሚለው ዊል ሔልም ሄንድሪክ ቫንሉን የሚሉት ድንቅ የታሪክ ፀሐፊ፤ ‹‹እኛ ዘመናውያን፣ የዓለም ‹ትልቁ› ሐገር ዜጋ በመሆናችን፣ ትልቅ የቲማቲም ወይም የድንች ፍሬ አምራች በመሆናችን እንኮራለን፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች የሚኖሩበት ከተማ ነዋሪ መሆን እንወዳለን፡፡ ደግሞም ከሐገሪቱ ውስጥ ተወዳዳሪ በሌለው ትልቅ የመቃብር ስፍራ ብንቀበር ምርጫችን ነው›› ሲል ይተቻል፡፡
በተቃራኒው፤ ‹‹የጥንታዊት ግሪክ ዜጋ የሆነ ሰው እንዲህ ስንል ቢሰማን፤ ግራ ሊጋባ ይችላል›› የሚለው ቫንሉን፤ የጥንታዊት ግሪክ ሰዎች የህይወታቸው ግብ እና የምኞታቸው ወደብ በሁሉም ነገር የተመጠነ ነገር ሆኖ መገኘትን ነው፡፡ ግባቸው ‹‹ልከኛው›› ወይም ‹‹መካከለኛው›› ነው -‹‹Moderation in all things››
ስለዚህ፤ በክብደት ወይም በስፋት ትልቅ መሆን ትርጉም አይሰጣቸውም፡፡ ‹‹ሳይረዝም - ሳያጥር፣ ሳይበዛ - ሳያንስ፣ ሳይቀላ- ሳይጠቁር›› ወዘተ ተብሎ ሊገለፅ የሚችለውን ነገር ይወዳሉ፡፡
አንድ ግሪካዊ፤ ‹‹እኛ ግሪካውያን ‹ምጥን› ነገር እንወዳለን›› ሲል፤ በሸንጎ ወግ ለማሳመር ወይም በግብዝነት መንፈስ ለመመፃደቅ አይደለም፡፡ አንድ ግሪካዊ ‹‹በነገርህ ሁሉ ምጥን ሁን›› ሲል ለላንቲካ አይደለም፡፡ ‹‹በነገርህ ሁሉ ምጥን ሁን›› የሚለው ሐሳብ ወይም መርህ፤ የአንድን ግሪካዊ ህይወት ከልደት እስከ ሞት የሚዘልቅ ጉዞ የሚገዛ እና በሁሉም የህይወት እንቅስቃሴዎች ገዢ የሚሆን የህይወት መመሪያ ነው፡፡
የሥነ- ፅሑፍ እና የኪነ - ጥበብ ሥራቸውን የሚገዛ ህግ ነው፡፡ ስለዚህ፤ ግሪካዊ ቤተ እምነቱን ሲሰራ፤ እንከን የለሽ እና ምጥን አድርጎ ነው፡፡ ወንዱ በሚለብሰው ልብስ፤ ሴቲቱ በምታደርገው የጆሮ ጌጥ ወይም የእጅ አምባር ይህ ህግ ይገለፃል። ወደ አምፊ ቴአትር ሲሄድ ተከትሎት ይሄዳል። እንደ ብረት የፀናን የ‹‹መልካም ሀሳብ›› ወይም የ‹‹መልካም ለዛ›› ህግን፤ (the Iron law of good taste and good sense) የሻረ ፀሐፌ ተውኔት ሲገጥማቸው፤ ከመድረክ ጎትተው እንዲያወርዱት የሚያስገድዳቸው ቀጭን ህግ ነው፡፡
ይህ ህግ፤ ሌላው ቀርቶ በፖለቲከኞቻቸው እና ባለዝና በሆኑ ጠንካራ አትሌቶቻቸው ባህርይ እንዲንፀባረቅ ይፈልጋሉ፡፡ እንደ አቦ ሸማኔ ሊታሰብ የሚችል አንድ ሯጭ፤ ስፓርታ ሄዶ፤ ‹‹በምድረ ግሪክ የሚኖር፤ ከኔ በበለጠ ረጅም ሰዓት በአንድ እግሩ ሊቆም የሚችል አንድ ሰው አይገኝም›› እያለ ጉራ ቢነዛ፤ ከከተማቸው ያባርሩታል፡፡ አንዲት ተራ ዳክዬ (goose) ልታስከነዳው በምትችልበት ጉዳይ ራሱን አኩራርቷልና ‹‹ውጣልን›› ብለው ያሳድዱታል፡፡
ይህን ስነግራችሁ፤ ምናልባት ‹‹ይገርማል›› ትሉ ይሆናል፡፡ ግን ጥያቄ መያዛችሁ አይቀርም፡፡ ‹‹እንከን የለሽ ሥራ ለመስራት እና ለምጥን ህይወት (Moderation) ይህን ያህል መጠንቀቅ ትልቅ ምግባር ነው፡፡ ግን በጥንታዊው ዘመን፤ እንዲህ ያለ የባህርይ ፅዳት ይዘው የሚገኙት ግሪካውያን ብቻ መሆናቸው ለምን ነው?›› ብላችሁ ብትጠይቁ፤ መልሱ ‹‹ሂዱ የግሪካውያን የኑሮ ሁኔታ ተመልከቱ›› የሚል ነው፡፡
የጥንታዊ ግብፅ ወይም የመሰጰጦምያ ህዝቦች፤ አንድ ቀን እንኳን በአይናቸው አይተውት በማያውቁት እና ከእነሱ ስንት ሺህ ኪሎ ሜትር ርቆ በሚገኝ ጨለማ በወረሰው ቤተ መንግስት ውስጥ በሚኖር እና ከስንት አንዴ አደባባይ ወጥቶ ለህዝብ በሚታይ፤ ማንነቱን በደንብ በማያውቁት ፍፁም ፈላጭ ቆራጭ በሆነ ንጉስ የሚገዙ ህዝቦች ናቸው፡፡
በተቃራኒው ግሪኮች፤ ፈላጭ ቆራጭ መንግስት ያልተጫነባቸው፤ መቶ በሚደርሱ ትናንሽ የከተማ መንግስታት የሚኖሩ ‹‹ነፃ ዜጎች›› (free citizens) ናቸው፡፡ በግሪክ ‹‹ትልቅ›› ሊባል የሚችለው ከተማ፤ በአሁኑ ዘመን ካሉ ትላልቅ ከተሞች አንድ ክፍለ - ከተማ ወይም መንደር ያነሰ የነዋሪዎች ቁጥር ያለው ነው፡፡
አንድ በኡር የሚኖር ገበሬ፤ ‹‹እኔ ባቢሎናዊ ነኝ›› ሲል፤ በጊዜው ምዕራባዊ የእስያ ክፍልን ጠቅልሎ ይገዛ ለነበረ አንድ ንጉስ፣ ግብር ከሚከፍሉ በሚሊዮኖች ከሚቆጠሩ ተገዢዎች አንዱ መሆኑን እየተናገረ ነው፡፡ ነገር ግን አንድ ግሪካዊ፤ ኮራ ብሎ፤ ‹‹እኔ አቴናዊ ነኝ›› ወይም ቴቢያዊ (Theban) ነኝ›› ሲል፤ ስለ አንዲት ከተማ እያወራ ነው፡፡ ይህች ከተማ፤ በአንድ ጊዜ የመኖሪያ አድራሻው እና ሐገሩ ናት፡፡ ለአንድ ግሪካዊ፤ በገበያ ሥፍራ ተሰብስቦ ውሳኔ ከሚያሳልፈው የከተማው (የሐገሩ) ህዝብ ፈቃድ ሌላ፤ የሚገዛለት ጌታ የለውም፡፡
ስለዚህ፤ አንድ ግሪካዊ ‹‹አባት ሀገሬ›› ብሎ የሚጠራት፤ እትብቱ የተቀበረባትን፣ አፈር ፈጭቶ - ጭቃ አብኩቶ፣ ድብብቆሽ እና እቴሜቴን ተጫውቶ ያደገባትን አጥቢያ ነው፡፡ በአክሮፖሊስ ቋጥኞች እንደ ዝንጀሮ እየዘለለ፤ በሽህ ከሚቆጠሩ አብሮ አደግ ሴቶች እና ወንዶች ልጆች ጋር እየተላፋ፤ ጉርምስናን ዘሎ ጉልምስናን የተቀዳጀበትን ቦታ ነው፡፡ በቅጽል ስማቸው ልትጠሯቸው እንደምትችሏቸው የክፍል ጓደኞቻችሁ፤ የድፍን የሐገሩን ሰዎች በቅጽል ስም ሊጠራቸው ይችላል፡፡ ግሪካዊ ‹‹አባት ሐገሬ›› ሲል፤ የእናቱ እና የአባቱ አጽም ያረፈባትን የተቀደሰች ምድር እየጠቀሰ ነው፡፡ ልጆቹ እና ምሽቱ በደህንነት ተጠብቀው የሚኖሩበትን እና ከፍ ባለ የግንብ አጥር የተከበበች ትንሽ መኖሪያ ቤቱ የምትገኝን ምድር እየጠቀሰ ነው፡፡
አንድ ግሪካዊ ‹‹አባት ሀገሬ›› ብሎ በፍቅር የሚጠራት፤ ምናልባት ከሦስት እና ከአራት ጋሻ የማይበልጥ ስፋት ያላትን እና በራሷ ምሉ የሆነችን ዓለታማ ምድር ነው፡፡ ታዲያ እንዲህ ያለ የመኖሪያ አካባቢ (ዓለም) በአንድ ሰው ግብር፣ ንግግር እና በሐሳብ ላይ እንዴት ተፅዕኖ ሊያሳድር እንደሚችል ማሰብ አስቸጋሪ አይሆንም፡፡
የባቢሎን፣ የአሲሪያ እና የግብጽ ህዝብ፤ ቢሄዱ - ቢሄዱ የማያልቅ የአንድ ትልቅ ግዛት ቁራጭ አካል በሆነ ክልል የሚኖሩ ናቸው፡፡ ስለዚህ፤ ማንነታቸው ለቁጥር በሚያታክት ብዛት ተውጦ፤ ከባህር እንደ ወደቀ ጨው ሟሙቶ ይጠፋል፡፡
ባቢሎናዊያን፤ የዲማው በዛብህ፤ አዲስ አበባ ሲገባ እንደ ገጠመው፤ ‹‹አባከና›› የመባል ፀጋን የሚያሳጣ ‹‹ስፋት እና ብዛት›› ባለው ግዛት የሚኖሩ ህዝቦች ናቸው። በተቃራኒው፤ አንድ ግሪካዊ የሚኖረው በልዩ ልዩ ትዝታ የተገመደ ትስስር ካለው የሀገሩ ሰው ጋር ነው፡፡ ከሚያውቃቸው እና ከሚያውቁት ጋር ይኖራል፡፡ እሱ፤ ሁሉም ሰው፤ ሁሉንም ሊያውቅ የሚችልበት ትንሽ ከተማ ዜጋ ነው፡፡ ስለዚህ፤ ሁሌም የሰላ አዕምሮ ባላቸው ጎረቤቶቹ እይታ ሥር ነው፡፡ ይህን ያውቃል፡፡ ምንም ነገር ቢሰራ ይታያል፡፡ ተውኔት ቢፅፍ ወይም የዕብነ - በረድ ሐውልት ቢያንፅ፤ ግጥም ቢገጥም፤ አለያም ዜማ ቢደርስ፤ ስለ ጥበብ ሥራዎች ባህርይ አብጠርጥረው በሚያውቁ የትውልድ ከተማው ወይም ‹‹የአባት ሐገሩ›› ነፃ ዜጎች፤ ሥራው ሁሉ በጥንቁቅ ዳኝነት እንደሚመዘን አሳምሮ ያውቃል፡፡ ይህ ዕውቀቱ ‹‹እንከን የለሽ›› ከሚባል ደረጃ የሚቀመጥ ሥራ እንዲሰራ ያተጋዋል፡፡ ከህፃንነቱ ጀምሮ እንደ ተማረው፤ ‹‹እንከን የለሽነት›› ያለ ‹‹ምጥንነት›› (moderation) ሊገኝ እንደማይችል በደንብ ይገነዘባል፡፡
እናም ወለም - ዘለም ማለትን በማይፈቅድ በዚህ ዓይነት የህይወት ጎዳና የሚያልፉት ግሪካውያን፤ በሁሉም መስክ የላቀ ሥራ ሰርቶ መገኘትን ተማሩ፡፡ አዲስ የመንግስት አስተዳደር ስርዓት ፈጥረው አፀኑ፤ አዲስ የሥነ- ፅሑፍ ቅርጽ ፈለስፉ፤ የሰው ልጅ በልቀት ተሻግሮ ሊያልፈው ያልቻለ አዲስ የሥነ- ጽሑፍ እሳቤ (Ideals) አበጁ፡፡ በዘመናዊ ከተሞች አራት ወይም አምስት ሪጋ (Blocks) ሊያሳርፍ ከሚችል ቦታ ያነሰ የቆዳ ስፋት ባላቸው ትናንሽ መንደሮች ውስጥ እየኖሩ ይህን ተዓምር ፈጠሩ፡፡
ታዲያ ወደ ኋላ ምን ሆነ?
ከክርስቶስ ልደት በፊት በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን፤ የመቄዶንያው ታላቁ እስክንድር፤ አያት - የቅድመ አያቱ ያኖሩለትን ወግ ሽሮ ዘመቻ ጀመረ፡፡ ዓለምንም ተቆጣጠረ፡፡ ጦርነቱን ብሎት ብሎት ሲሰለቸው፤ ኢዩር የግሪክ ሊቃውንት የሰጡትን የዕውቀት ፀጋ፤ ለጠቅላላው የሰው ዘር ማዳረስ አለብኝ አለ፡፡
ያን ድንቅ የዕውቀት አዝመራ፤ ከትናንሾቹ የግሪክ ከተሞች እና መንደሮች እየሸመጠጠ ወስዶ፤ አዲስ ባቀናው ግዛተ - አጼ (Empire) በሚገኙ የነገስታት መኖሪያዎች እየዘራ፤ ዘሩን ለማፅደቅ ታገለ፡፡
ታዲያ የለመዱትን ቤተ እምነታቸውን ለማየት ከማይችሉበት ሩቅ ስፍራ የሄዱት፤ አሳምረው የሚያውቁትን እና ጆሯቸው የለመደውን ድምጽ ከሚሰሙበት የሐገራቸው ጎዳና በጣም ርቀው የሄዱት ግሪኮች፤ ያን ልብ የሚፈነቅል ደስታቸውን አጡ፡፡ ጥንታዊ የከተማ መንግስቶቻቸውን ከሁሉ የላቀ ሆኖ እንዲታይ ለማድረግ ደፋ ቀና ሲሉ፤ የዕደ ጥበባቸው እና የአዕምሯቸው ውጤት የሆኑ ድንቅ ሥራዎቻቸውን ሲሰሩ ንቁ መንፈስ እንዲይዙ ያደረጋቸውን ነባር አስተሳሰብ በአንድ ጊዜ ጣሉት፡፡ ሲያልቅ አያምር እንዲሉ፤ ለትልቅነት ያበቃቸውን ያን አስተሳሰብ ሲተው፤ ግሪካውያን ቅራሬ በሆነ ሥራ (second- rate work) የሚረኩ፤ ውርዴ ዕደ ጥበባውያን (cheap artisans) ሆነው ቀሩ፡፡
የጥንታዊ ሔለናውያን ትናንሽ የከተማ መንግስታት ነፃነት ሲፈርስና፤ የአንድ ትልቅ ሐገር ቁራጭ አካል ክፍል እንዲሆኑ በተደረገ ማግስት፤ ጥንታዊው የግሪካውያን መንፈስ ሞተ፡፡ ያ ግሪካዊ መንፈስ፤ ከዚያ ጀምሮ እስከ ዛሬ ሞቶ እንደ ተቀበረ ቀርቷል፡፡ ‹‹በነገርህ ሁሉ ምጥን ሁን›› የሚል ወርቃማ ህጓን የተወችው ግሪክ፤ ብድር አብዝታ ወስዳ በማጣጣር ላይ ትገኛለች፡፡ ከእነ አቴና ወይም ስፓርታ ጋር ስትነፃፀር ትልቅ ግዛት ያላት ቢሆንም፤ ትንሽ ሐገር ነች፡፡
ይህን የግሪክ ታሪክ ያወሳሁት፤ ‹‹እንዲያው ለጨዋታ›› ብዬ አይደለም፡፡ እንዲያውም ‹‹አስተምራለሁ›› ብዬ ነው። ‹‹ሁሉም ነገር በልክ›› ከማለት የበለጠ ምን ትምህርት ይኖራል፡፡

Published in ጥበብ

መሀል ከተማ ዘይኔ ሻይ ቤት ቁጭ ብዬ ማዶውን የጓደኛዬን የእነ መላኩን የቃጫ መጋዘን ሣይ አብሬ ብዙ ነገር አያለሁ፡፡ የጫት ገበያተኞች ወከባ፣ የሊስትሮዎች ሣቅና ተረብ፣ የመንገደኞች ወዲያ ወዲህ ማለት፡፡ ልቤ ግን አሁንም ተመልሶ መላኩ ጋ ነው፡፡ ዛሬ መላኩ ካገኘኝ አይላቀቀኝም፡፡ በዚህ ሰዓት ደግሞ የትም አይሄድም፡፡ ጠዋት ትምህርት ቤት በሩቅ አይቼው ነበር፡፡ ለምን እንደተጣደፈ ባላውቅም ተደብቆ ሲፎርፍ አይቼዋለሁ፡፡ ለነገሩ ፎርፌ ሕይወቱ ነው፡፡
እኔም ትምህርት ቤት የምሄደው የእርሻ አስተማሪዬ ያዘዙኝን ለመፈፀም ነው፡፡ መምህራችን ያከፋፈሉንን መደብ በደንብ ካልቆፈርንና ለዘር ካላመቻቸን ማርካችን ይቆረጣል፡፡ ያንን ፈርቼ ነው፡፡ ያለፈው ሴሚስተር ውጤቴ ጥሩ ስላልነበረ ማስተካከል አለብኝ፡፡ የክፍል ደረጃዬ ሲቀንስ ደግሞ እቤት ውስጥ መከራ ይጠብቀኛል፡፡ ከዚያ መከራ ለማምለጥ ነው አሁን ከመላኩ ጋር መከራ የገባሁት። አሁን ካገኘኝ ይጣላኛል፡፡ ሳያየኝ በአንዳች ዘዴ ነው መጋዘናቸውን ማለፍ ያለብኝ፡፡
መላኩ ደግሞ አባቱ ወንበር ላይ ተቀምጠው በሚዛን ቃጫ እየመዘኑ ከሚገቡበት ቦታ አይጠፋም። ርስቱ ነው፡፡ አንዳንዴ ቢጠፋም ለተንኮል ነው። ሰው ጓሮ ሄዶ ኮክና ዘይቱን ለመስረቅ ወይም ሸንኮራ ለመስበር ነው፡፡ ለትምህርቱ ግድ የለውም። ከጓደኞቹ እየኮረጀ ነው አራተኛ ክፍል የደረሰው፡፡ አባቱም እንደእርሳቸው እንዲነግድ ይሆን ባላውቅም አይቆጡትም! እንደ ልቡ ነው፡፡
መጋዘኑ ወደ ትምህርት ቤት ማለፊያ መንገድ ላይ መሆኑ ደግሞ ከፋ፡፡ ፉርኖ የምትባል ያክስቱን ልጅ ስመሀታል ብሎ ነው ለመደባደብ ዘራፍ የሚለው፡፡ ሠፈሩ ስለሆነ እንጂ እኔም በሠፈሬ ለርሱ አላንስም፡፡
“እኔ ፉርኖን ቁመቴ የት ደርሶ ነው የሣምኳት?” ስለው “በረንዳችሁ ላይ ቆመህ ነው ሰምቻለሁ!” አለኝ፡፡ ይህን ያቃጠረው ማን እንደሆነ አውቃለሁ። አንድ ቦቅቧቃ ጓደኛችን አለ፡፡ ለርሱ ዋጋውን እሰጠዋለሁ፡- ፊቱን በጥፊ ሳጮለው ቀይ ፊቱ ሣንባ ይመስላል፡፡ ከዚያ እንባው ይፈስሳል፡፡ ቁመት ብቻ ነው እሱ ደሞ! ሴት መልክ! ትዝ ሲለኝ ብሽቅ አልኩ።
መጋዘኑ ደጅ መላኩ የለም፡፡ ግን አንደኛው ወንድሙ አለ፡፡ ሁሉም ተሣዳቢ ናቸው፡፡ ባይመቻቸው እንኳ ምላስ ያወጣሉ፡፡ ካልሆነም በወንጭፍ ጠጠር ይሰድዳሉ፡፡ በትምህርት ቤት የጓሮ መግቢያ መሽሎኪያ ቀዳዳ አለ፡፡ ግን ዘበኞቹ ካገኙኝ አበሳ ያስቆጥሩኛል፡፡ በተለይ ጋሽ ጦቢያ ጆሮ ይተለትላል፡፡ በዚያ ቁመቱ ጢሙን ጠቅልሎ ሲያስፈራ! ጠመንጃማ ከእጁ አይለይም፡፡ እድሜው ረጅም ነው፤ ጋሽ ጦቢያ ሸሚዝ ለብሶ፣ የወታደር ጫማውን ተጫምቶ፣ እግሩን ብድግ ብድግ እያደረገ በዋናው መንገድ ሲያልፍ አየሁት፡፡ ነፍስ እንደያዘው ሰው ሮጬ “ጋሽ ጦቢያ” አልኩት፡፡
“ምን ሆነሃል?” አለኝ፡፡ የተቆጣ መስሎኝ ነበር፣ ፈገግ አለ፡፡ ጥርሶቹ እንዲህ ያምራሉ እንዴ?
“አይ ወደ ትምህርት ቤት ልሄድ ነው፡፡”
“ና - ታዲያ” አለና አንድ እጁን ዘረጋልኝ፡፡
እጄን ይዞኝ “ከልጆች ተጣልተሃል እንዴ?” አለና ሳቀ፡፡ እኔ አሁንም መላኩን እያሰብኩ ነው፡፡ በደግ ቀን ይጋብዘኛል፡፡ ስንጣላ ደሞ ሰይጣን ነው መላኩ። ፀጉሩ ቁርንድድ፣ አፍንጫው ድፍጥጥ ያለ ነው፡፡
ቀስስ ብዬ ከጋሽ ጦቢያ ጋር ሳልፍ ታናሽ ወንድሙ በአይኑ ፈልፍሎ አየኝ፡፡ ጋሽ ጦቢያ እያለ እንደማይነካኝ አውቃለሁ፡፡ ግን አጥር ዘልሎም ቢሆን ሊመጣብኝ ይችላል፡፡ ሲለው ያቺን ተፈሪ ኬላን ዳር እስከ ዳር ያምሣታል፡፡ ቢገረፍም ግድ የለው፡፡
ትምህርት ቤት ግቢ ስገባ ጨፈቃ ነገር ልቆርጥ አስቤ ነበር፡፡ ግን አልተመቸኝም፡፡ በዚህ ሃሳብ ውስጥ ሆኜ ወደ እርሻ መደቤ እየሄድኩ እያለ የጋሽ ጦቢያ ድምጽ አቋረጠኝ፡፡
“ምን ልታደርግ ነው የመጣኸው?”
“የእርሻ ቲቸሬ የእርሻ መደቤን ኮትኩት ብለውኝ ነው፡፡”
“ታዲያ መኮትኮቻ የታል? በጥፍርህ ልትኮተኩት ነው፡፡”
“በል ና መኮትኮቻ ውሰድ!” ብሎ ይዞኝ ሄደ። እንደ ፌንጣ ወደሰማይ ብዘልል ደስታዬ ነው፡፡ አሁን መላኩ ቢመጣ እንኳ ግድ የለኝም፡፡ ዋጋው እሰጠዋለሁ፡፡ ደረቴን ነፋሁ፡፡ ከብዙ መቆፈሪያዎች አስመርጦኝ ባለ ሁለት ምላስዋን መኮትኮቻ ተቀበልኩ፡፡
“እንደ ጨረስክ መልስ ታዲያ…”
“እሺ ጋሼ!” ብዬ በረርኩ፡፡
በአንድ በኩል የእርሻ መምህራችንን ሃሳብ በመፈፀሜ፣ በሌላ በኩል ከመላኩ ስጋት በመዳኔ እየተደሰትኩ ሄጄ ኩትኳቶ ጀመርኩ፡፡ መደቤን ቆንጆ አድርጌ አሣመርኩና የመምህሬን ፈገግታ አሰብኩት። ከጥቁር ፊታቸው ታች እሸት በቆሎ የሚመስሉ ጥርሶቻቸውን አሰብኩ፡፡ በአለንጋ አይነኩኝም፤ ወይም ልምጭ ቆርጠህ አምጣ አይሉም፡፡ ፈገግ ብለው ትከሻዬን ቸብ ቸብ ያደርጉኛል፡፡
የመላኩ ነገር ግን በዛሬ ብቻ የሚያበቃ አይደለም፤ አንላቀቅም አውቃለሁ፡፡ ችግሩ ግን ትምህርት ቤት የምሄደው በእነርሱ መጋዘን በር አልፌ ነው፡፡ መቸም ለምን ነገረኛ እንደሆነ ባላውቅም በጉልበት ግን አላንሰውም፡፡ የርሱ ክፋት ዱላ፣ ብረት፣ ድንጋይ መያዙ ነው፡፡ ሰሞኑን ለፉርኖ ጠበቃ ሆኖ እኔን ጓደኛውን ማወኩ አልገባኝም። ፉርኖ ያክስቱ ልጅ ብትሆንና እኔ ብስማት ምን አገባው? ያንዱን ጓደኛ እህት የሚያገባት ሌላ ሰው መሆኑን እንኳ አያውቅም፡፡
ሰማዩ እንደመጨለም፣ እንደማጉረምረም አለ። ከከተማው ግራና ቀኝ የተንጠራሩት ተራሮች ፊታቸውን ማጥቆር ጀመሩ፡፡ እኔም ኩትኳቶዬን ጨርሼ መኮትኮቻውን አሥረክቤ ለመውጣት ወደ ጋሽ ጦቢያ ፈጠንኩ፡፡
ጋሽ ጦቢያ ካፖርቱን ግጥም አድርጐ ለብሶ፣ ፊቱን በፎጣ ነገር ጠቅልሏል፡፡ በዚያ ላይ ጠመንጃውን እንዳነገተ ነው፡፡ ጠመንጃውን ለምን እንደማይለቅ ግራ ይገባኛል፡፡ ፈሪ ሣይሆን አይቀርም፡፡
“አመሠግናለሁ ጋሽ ጦቢያ” አልኩና ሰጠሁት። ዞር ቢልልኝ በጓሮ አጥር በኩል ሾልኬ መላኩ ሳያገኘኝ ላመልጥ ፈልጌ ነበር፡፡ ግን አልለቀቀኝም እስከዋናው በር ተከተለኝ፡፡
ከግቢ ከወጣሁ በኋላ ትንሽ ቆሜ አመነታሁ፡፡ እንዴት አድርጌ የእነመላኩን መጋዘን ልለፍ? በዓይኔ ከወደ በንቆቃ በኩል የሚመጣ ሰው ፈለግሁ፡፡ በንቆቃ ወንዝ በዲላ መስመር ነው፡፡ አንዳንዴ ከዚያ በኩል የሚመጡ ተማሪ ጓደኞች አሉኝ፡፡ እነርሱን ጠበቅሁ፡፡ ማንም አልመጣም። ለክፉም ለደጉም አልኩና አንድ ረዘም ያለ ሹል ድንጋይ በኪሴ ያዝኩ፡፡
ቀጥዬ ማዶውን በሰዎች በረንዳ እየታከክሁ ሄድኩ፡፡ ከቤታቸው ፊት ለፊት አካባቢ ፖሊስ ጣቢያ አለ፡፡ እዚያ ደረስኩና ቆምኩ፡፡ ፖሊሱ ምትኩ ቆሟል፡፡ እሱም ፊቱን አስቀርቶ ጭንቅላቱን በጃኬት ቆብ ጠቅልሏል፡፡ ቀስ ብሎ አየኝ፡፡
“ምን ታረጋለህ አንተ ልጅ?”
“ምንም!”
“ዝናም ሳይመጣ ወደቤትህ አትሄድም!”
“አይ መላኩ የሚባል ነገረኛ ልጅ አለ እዚያ!”
“ፈርተህ ነው? በልና” ብሎ እጄን ያዘና አሳለፈኝ፡፡
እኛ ሠፈር መጥቶ እትዬ አበባየሁ ጠጅ ቤት ይጠጣል። ለነገሩ እዚያች ትንሽ ከተማ ውስጥ የማይተዋወቅ የለም። ባለሱቁ፣ ባለዳቦ ቤቱ፣ ባለቡና ቤቱ፣ ልብስ ሰፊዊና አናጢው ሁሉም ይተዋወቃል፡፡
የነመላኩን መጋዘን እንዳለፍኩ ወደ ቤት በረርኩ። ይሁን እንጂ ቤት ሄጄም ልቤ አላረፈም፡፡ ከመላኩ ቁጣ የማመልጥበትን ዘዴ አሰላሁ፡፡ ወደ ማዕድ ቤት ገባሁና ትልቅ ምሥማር ፈለግሁ፡፡ ለክፉ ቀን የማስቀምጣቸው ብረቶች አሉኝ፡፡ አሰስኩ፡፡ እናቴ ሳትመጣ ሁሉን ለማጠናቀቅ ተፍ ተፍ አልኩ። ያገኘሁት ምስማር ተስማሚ ነበር፡፡ ጫፉን እንደ ሴንጢ ጠፍጥፌዋለሁ፡፡ በቃ ይቺ ለመላኩ ልክ ማስገቢያ ናት፡፡
ወደ ኪሴ ከተትኳት፡፡
ዝናቡ ዶፉን አወረደው፡፡ ፊት ለፊቴ በረንዳ ላይ ቆሜ ማዶውን ወዳሉት ተራሮች አየሁ፡፡ ጨልመዋል፡፡ ጓደኞቼም በየቤታቸው ተከትተዋል። በየበረንዳው ፍዝዝ ብሎ ዝናቡን ከሚያየው ሰው በቀር መንገዱ ባዶ ነው፡፡
ዝናሙ ሳያባራ ቀጠለ፡፡ ማምሻ ላይ ብቻ ጨለምለም ሲል ቀስ እያለ አባራ፡፡ ሰውም ከትምህርት ቤት እንደተለቀቀ ተማሪ በየአቅጣጫው ተመመ፡፡
እኔም ምሥማሬን በኪሴ ይዤ ተንቀሳቀስኩ፡፡
ነጐድጓዱ ሰማይ እየቧጠጠ፣ ሆድ እያባባ ሲቀጥል፣ እናቴ ሻማ ግዛ ብላ ወደ ሱቅ ላከችኝ፡፡ የልጅ ባርኔጣዬን አናቴ ላይ አድርጌ ዶፍ ከመዝነቡ በፊት በረርኩ፡፡ ቢሆንም አልዘነጋሁም፡፡ የተሣለ ምስማሬን በግራ እጄ ጨብጫለሁ፡፡ አሁንም ልቤ ጥርጣሬውን አልተወም፡፡
ሱቅ ገብቼ ስወጣ ሰማዩ የተንጓጓ፣ መብረቅ እላዬ ላይ የወደቀ መሠለኝ፡፡ ጆሮ ግንዴ ጮኸ፡፡ መሬት ላይ ተዘረርኩ፡፡ በእጄ የያዝኩት ሻማና ምሥማር ወደቀ፡፡ በጆሮዬ ድምጽ እንደ ሕልም ይሰማኛል። ሁለተኛ እንኳን ከንፈሬን እግሬን አትስማትም፡፡ የፉርኖ መሆን አለበት፡፡ በመሸነፌ አፍራ ይሆን?

Published in ጥበብ
Saturday, 27 June 2015 09:36

ወፈፌው

አንገቱ ላይ የተንጠለጠለውን ገመድ የሙጥኝ እንዳለ ነው፡፡ ቁርጠኛ ውሳኔውን ለማጨናገፍ የሚንከወከው ድንገቴ ቢመጣ  ሳይቀድመው እንደሚቀድመው ተማምኗል፡፡ አንዲት እራፊ ጨርቅ ብቻ ነች ኃፍረተ - ሥጋውን የሸፈነችው፡፡ ገመዷ ከቦታዋ መኖር አለመኖሯን እያሰለሰ ይሰልላታል፡፡
ጠደፍ ጠደፍ እያለ ሠፊውን ጎዳና በሰጎን ቅልጥሞቹ እየመተረ ማቋረጥ ጀመረ፡፡ ግራ ቀኙን አልተመለከተም፡፡ ሲከንፉ የመጡ አውቶሞቢሎች የወፈፌው በጎዳናው ላይ ድንገት መደንጎር ቢያጥበረብራቸው እንደ ወታደራዊ ዘብ ቀጥ ብለው ቆሙ፡፡ ጎማቸው ከጎዳና ጋር ክፉኛ ተሳሳመ፤ አካባቢውን ለጆሮ በሚቀፍ ድምጽ አወኩት፡፡
“ይሄ ጋኔል የሰረረው…ደርሶ…ሰበብ..ሊሆን ነው..እንጂ“ ከወዲያ ማዶ ያሉት የባንክ ቤቱ ጥበቃ አንቧረቀ፡፡
ወፈፌው ሁኔታውን ከመጤፍ አልቆጠረውም። ወደ ግራ የሚታጠፈውን የአስፓልት ጎዳና ያዘ፡፡ ሕዝበ አዳም የዕለት ጉርሱን ሊያበስል በየአቅጣጫው ይተማል፡፡ ይህ ጭንቀት ከወፈፌው ጫንቃ ላይ ከወረደ ሰነባበተ፡፡ ስለ ዕለት ጉርስ፣ ስለ ጎን ማረፊያ የሚያውጠነጥነው ናላው ታውኳል፡፡
ፍጥነቱን ከቅድሙ የባሰ ጨመረ፡፡ አላፊ አግዳሚው በሁኔታው ተደናግጦ ጥጉ ጥጉን እየያዘ እያሳለፈው ነው፡፡
የወፈፌው ጥድፊያ እንደው በዋዛ አይደለም። ነፍሱን በእጅ ይዞ የሚካለበው ከሚያሳድደው መንፈስ ለማምለጥ ነው፡፡ ከደቂቃዎች በፊት ሠፊ ሆድ ካለው ጨለማ ዋሻ ውስጥ ቁምስቅሉን ሲያይ  ነበር፡፡ ምርኮው ያደረገው ጋኔን የእሳት ጅራፉን ከገላው ላይ ማሳረፍ ከሰለሰ ገና ጥቂት ሰዓታት ነው የነጎዱት፡፡ አንገቱ ላይ የሸመቀቃት ገመድ ልክ እንደጨቅላነቱ ክታብ ከሳጥናኤል ጡቻ የሚመክትባት ጋሻው ሆናለታለች፡፡ ገመዷን ጠበቅ አደረጋትና ፍጥነቱን ጨመረ፡፡
ትንሽ እልፍ እንዳለ ትከሻዋን እየሰበቀች፣ ዳሌዋን እያማታች የምትውረገረግ መልከመልካም ሴት ከአላፊው አግዳሚው ልቃ ከአይኑ ገባች፡፡ ይህቺን ሴት በእዛ በከርሳም ዋሻ ውስጥ በደንብ ያውቃታል። ከሰዓታት በፊት የሳጥናኤል ቀኝ እጅ፣ የእርሱ ጣውንት ነበረች፡፡ አለንጋ ጣቶቿ የዋሻውን እሳት ለማንተርከክ ነው የሰለጠኑት፡፡ በረገጠበት ቦታ ሁሉ እንደጥላው የምትከተለውን ባላንጣውን አንድ ነገር ማድረግ እንዳለበት አሰበ……ደመነፍሱ ፈጥኖ እርምጃ እንዲወስድ ወተወተው፡፡
“እዚህ ደግሞ ምንድን ነው የሚያልከሰክሳት፣ይህቺ ጆሮ ጠቢ፣ የሳጥናኤል መልእክተኛ፤ ሳትቀድመኝ ልቅደማት?” በውስጡ አጉተመተመና ወደ ልጅቷ ተንደረደረ፡፡
ድንገት አቅጣጫ ለውጦ ጎዳናውን ለመሻገር እግሩን ሲሰነዝር ሲከንፍ ከመጣ መኪና ጋር ተሳሳመ፡፡ አየር ላይ ተንሳፍፎ በአርበ ሰፊው ጎዳና ላይ እንዳይሆኑ ሆኖ ተነጠፈ፡፡ በደም የተለወሰውን በድን አላፊ አግዳሚው እንደ ንብ ሠራዊት ከበበው፡፡
*   *   *
ወፈፌውን ዓለም ከተፋችው ሰንብታለች። አሁን ሲበር የመጣው ከአማኑኤል ሆስፒታል ሾልኮ ነው፡፡ የሆስፒታሉ ታካሚ መሆን ከጀመረ መንፈቅ አልሞላውም፡፡ ፊት ወሰድ መለስ ነበር የሚያደርገው፡፡ ኋላ ላይ ወሰድ መለሱ ወደ ለየለት እብደት ተለወጠ፡፡
የወፈፌነቱ አባዜ ገና ኮሌጅ እንደበጠሰ ነው የተጠናወተው፡፡ ግብሩ ሁሉ ከዕድሜ እኩዮቹ ጋር አይገጥምም ነበር፡፡ ቢጤዎቹን፣ የእድሜ አቻዎቹን መምሰል ተሳነው፡፡ እንደ ኮብል ድንጋይ ተጠፍጥፎ ላለመበጃጀት እባጭ ሆኖ ተውተረተረ፡፡
የቀለም መምህሩ ልክ እንደፈሪሳዊያን በቃላት የሚታበይ ነው፡፡ ከአአምሮው በመሰገው መናኛ እውቀት ክፉኛ ይደለላል፡፡ ከእዚህ ድብታ መሓል ለአመል ዘለግ ብሎ የሚገዳደረው ወፈፌው ነበር። መምህሩ በአራት ነጥብ ያሰረውን ፍሬ ሐሳቡን ወፈፌው በጥያቄ ምልክት ይፈተዋል፡፡
“ይህ ትውልድ ለመቀበል እንጂ ለመጠየቅ አልታደለም…..“ይላል ፈሪሳዊው መምህር ገና ክፍል እንደገባ፤ ከወፈፌው ሊቃጣ የሚችልን ፈታኝ ጥያቄ ለመመከት፡፡
ቀናት በገፉ ቁጥር የወፈፌውና የፈሪሳዊው መምህር መቃቃር እየከፋ ሄደ፡፡ እሰጣ ገባው ወፈፌው ላይ ሌላ መዘዝ ይዞ ብቅ አለ፡፡ በአምስት አመት የሚገባደድን ትምህርት እስከ ሰባት ዓመት አስዘለቀው፡፡ ኮሌጅ በረገጠ በሰባት ዓመቱ ቆብ ለመድፋት በቃ፡፡
ቆብ በደፋ ማግስት ከአንድ አገልግሎት ሰጪ መ/ቤት ተቀጠረ፡፡ ሳይውል ሳያድር ወንበር ማሞቁ አጥወለወለው፡፡ መምህር በስንት ጣዕም ብሎ ከአንድ ኮሌጅ እጅግም በማያወላዳ ደሞወዝ ቀለም ማስቆጠርን ሥራዬ ብሎ ተያያዘ፡፡ ከእዚህ ቀደም ሲቀናቀነው በነበረው መምህሩ እግር ተተክቶ ትውልድ የመቅረጽ ድርሻውን እየተወጣ ሰኔ ግም እስኪል ጠበቀ፡፡ የጠናወተው ልክፍት ግን ከዚህ በላይ ሊያዘልቅው አልቻለም፡፡
የወሰድ መለሱን ስብዕናውን ቀስ በቀስ እያጣ እንደሆነ ሲገባው ጥቂት አወጣ አወረደ፤ እና የቀለም ተማሪዎቹን ተሞክሮ በማይታወቅ ሃዲድ ላይ ሊያነጉዳቸው ወሰነ፡፡
ክፍለ ጊዜውን ባልተመለደ ሁኔታ በሁለት እኩሌታ ከፈለው፡፡ በመጀመሪያ ክፍለ-ጊዜ ለፈተና በደንብ የሚያዘጋጅ ፍሬ-ሐሳብን ከላይ እስከታች ይተረትራል፡፡ በተቀረው ክፍለ ጊዜ ደግሞ ንቃትን በሚያበረታ ፍሬ ሐሳብ ላይ ይጠበባል፡፡ በሰላሳ ደቂቃ ያስተማረውን ፍሬ ሐሳብ በተቀረው ሰላሳ ደቂቃ ያፈራርሰዋል፡፡
“ዕውቀት እና ሽልማት ለየቅል ናቸው፡፡ ሽልማት ካላችሁ ቀዳሚውን …. እውቀት ካሰኛችሁ ደግሞ የኋልኛውን መምረጥ የእናንተ ፋንታ ነው” የየዕለቱን ማብራሪያ ከመጀመሩ በፊት ከአንደበቱ የሚፈልቅ አባባል ነው፡፡
የወፈፌው የመማር፣ማስተማር ስልትን በበጎ የሚተረጉም ወገን ግን ጠፋ፡፡ ይብስ ብሎ የኮሌጁ ቀለም ቆጣሪ በአንድነት አብሮ የትምህርት ገበታውን አራቆተው፡፡ ሳይውል ሳያድር የኮሌጁ አስተዳዳሪዎች ትውልድ እየገደልክ ነው ብለው ወፈፌውን መምህር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አሰናበቱት፡፡ በፈሪሳዊው መምህር ግብር ተመዝኖ ትውልድ ገዳይነቱ ታወጀ፡፡
ሥራ አጥ ሆኖ ወዲህ ወዲያ መንከላወስ የአዘቦት ግብሩ መሆን ከጀመረ ቀናት አለፉ፡፡ ሲያገኝ ይበላል፣ ሲያጣ ድፍት ብሎ ያድራል፡፡
ቀኑ ዕለት ሰንበት ነው፡፡ ደርሶ  ጠጣ ጠጣ የሚል ስሜት  ሽው አለበት፡፡ አንድ ሁለት ለማለት ወደ አንዲት ባለጉልላታም ጠጅ ቤት ጎራ አለ። ቤቷ ብርድን እና ድብርትን በሸሹ እድምተኞች ተጨናንቃለች፡፡ ገና ከመቀመጡ ጠጅ ቀጂው በሆድ ዕቃዋ ጥም ቆራጭ ያቆረች ከርሳም ብርሌን ኳ….ኳ አድርጎ ከፊቱ ጎለተለት፡፡ ዓይነ ግቡዋን ብርሌ ወደ አፉ አስጠጋት፡፡ በሆድ ዕቃዋ ያዘለችውን ጥም መቁረጪያ ወደ ጉሮሮው ላከው፡፡ የእርካታ ስሜት መላ ሰውነቱን ሲወረው ተሰማው፡፡
የነተበ የወታደር ዩኒፎርም የለበሰ ጎስቋላ ሰው፣ በጠጅ ቤቱ ሁካታ ላይ የራሱን ነጠላ ጩኸት እያከለ ነው
“ቢንጎ ቢንጎ፤ ቢንጎ ለባለዕድል” ድምጹን ከሁካታው መሃል ዘለግ ለማድረግ ይታገላል፡፡
ጥርስ አልባ ድዳቸው እንዳይታይ በተከናነቡት ነጠላ ጠርዝ የሚመሸጉ ጠና ያሉ ሴት ከቢንጎ አጫዎቹ ላይ በርከት ያሉ ዕጣዎቹን ለመሸመት ቅድሚያውን ወሰዱ። ከሴትየዋ ጋር እልህ የተጋቡ የሚመስሉ ሌሎች አቻ ጠጪዎች ቀሪዎቹ እጣዎች ላይ ተረባረቡ። አጫዋቹ እጁ ላይ የቀሩትን ጥቂት እጣዎች ለባለዕድለኞች ለመሰዋት ግራ ቀኙን እያማተረ ድምጹን ያለ ስስት ማውጣቱን ቀጠለ፤
“ቢንጎ  ቢንጎ ለባለ ዕድል” ይላል
ወፈፌው አገጩ ላይ ዘርዘር ብሎ ከበቀለው ጺሙ መካከል መለሎ የሆኑትን መርጦ በጣቶቹ መሀል  እየፈተለ ለቀሪዎቹ ዕጣዎች እጁን ዘረጋ። ቢንጎ አጫዋቹ የተቀበላቸውን ጥንድ ሽልንጎች ከሌሎች  የሽልንግ ቤተሰብ ጋር እየደመረ ፊቱን ፈንዲሻ አደረገለት።
ኮርነር ላይ የመሸገው ጠጅ አንቆርቋሪ ከጠጪው በተለየ ትኩረት የመስረቅ ኃይል አለው፡፡ ሁካታውን እንደ ጥዑም ዜማ እየጣጣመ መጽሓፍ ይገልጣል፡፡ ብርሌ የጨበጡ እጆቹ የመጽሓፍ ገላን ለመደባበስ አልሰነፉም። ከገለጠው መጽሐፍ ትንሽ ገጽ ያነበንብና መልሶ ይከድናዋል፡፡ የመጽሐፉ ልባስ ግማሽ አካሉ የለም፡፡ ጣቱ ያረፈበት ገጽና የሽፋኑ ስዕል ሳይገጥምበት አልቀርም፡፡ ወደ ልባሱ አይኑን ወርወር ያደርግና መልሶ ጭንቅላቱን  ግራና ቀኝ  ያማታል፡፡
 “የሃቅ..መግቢያ ልክ እንደ የቀበሮ ጉድጓድ ጠባብ ናት …” አለ በስሜት ተውጦ ከሆነ ገጽ ላይ ሲደርስ። ሰሚ ያገኘ አይመስልም፡፡ ብርሌውን እንደመፈክር ወደ ላይ ከፍ አደረገና በፍቅር ከብርሌዋ ጋር ከንፈር ለከንፈር ተሳሳመ፡፡ ጠረጴዛውን በኃይል ደቃና አባባሉን ደገመው፤
“የሃቅ መግቢያ ልክ እንደ የቀበሮ ጉድጓድ ናት” የአሁኑ ድምጹ ግን አለቅጥ ዘለግ ብሏል፡፡
ከእርሱ ገጥ ለገጥ ወደ ተሰየመ ጎልማሳ ሰው እየጠቆመ፤
“ለእንደ አንተ…አይነቱ ሴት አውል…ግን...መግቢያው የመርፌ ቀዳዳ  ይሆናል” አለ  የድምፁን ጉልበት ሳይቀንስ።
ጎልማሳው ቃል አልተነፈሰም፡፡ ፊቱን ወደ ወለሉ ዘመም አድርጎ በውስጡ አጉተመተመ፡፡
‘ባለጠጋ መንግሥተ ሰማያትን ከሚወርስ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፍ ይቀላል…..አትልም…… አንድ ፊቱን” ወፈፌው አከታትሎ በጨለጠው ጠጅ ተበራትቶ አንደበቱን አፍታታ፤
“በቀዳዳው ለመሹለክ …..ከእዚህ ሴት አውል..ይልቅ… እኔ ከሲታ ነኝ….አሃሃሃሃሃሃሃ”
ጠጪው አብሮ አውካካ፡፡ የጎልማሳው ገጽታ ከመቅጽበት ከሰለ፡፡ የቀረበለትን ጠጅ በአንድ ትንፋሽ ጨለጠና ፊቱን ጨፍግጐ መሬት መሬቱን እያየ ትካዜ ውስጥ ገባ፡፡ ድንገት ብርሌውን አንስቶ ወደ ሰውዬው ግምባር ተኮሰው፡፡ የተተኮሰው ብርሌ ግን የሰውየውን ግምባር ሸሽቶ ከወፈፌው መስቀለኛ ላይ ውኃ ሆነ። ከእዚህ በኋላ ወፈፌው ራሱን ያገኘው አማኑኤል ሆስፒታል ውስጥ ነው፡፡ የብርሌዋ ገላ የወፈፌውን የአዕምሮ ድር ለመበጣጠስ ጊዜ አልወሰደባትም፡፡ በቋፍ የነበረው ማንነቱ ከእነአካቴው ወደ ለየለት እብደት ተለወጠ፡፡ የለየለት እብድ ሆነ፡፡
*  *  *
ይሄኛው የመኪና አደጋ የትኛውን ድር ይበጣጥስ ይሆን… ወይስ ከእነካቴው የሕይወቱን ድር ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ በጣጥሶ ይገላግለዋል?
በምናብ የፈጠረውን ሴጣን ሲሸሽ በአካል እየከነፈ የመጣው ሴጣን ገላፊቻ አለው፡፡ በአካል የመጣን ሴጣን አማትበው አይርቁት ነገር!

Published in ልብ-ወለድ

በቀድሞ አጠራር በሲዳሞ ክ/ሀገር በቡሌ ወረዳ የተወለዱት ደራሲና ጋዜጠኛ ሽፈራው መንገሻ ባደረባቸው ህመም በአገር ውስጥና በውጭ በህክምና ሲረዱ ቆይተው ባለፈው ሰኔ 12 በ75 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩ ሲሆን በነጋታው የቀብር ሥነስርዓታቸው በቅዱስ ዮሴፍ ቤ/ክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡
ለረዥም ዓመታት በተለያዩ የመንግስት መ/ቤቶች ያገለገሉት አቶ ሽፈራው፤ በማስታወቂያ ሚ/ር ፕሬስ መምሪያ የሳምንታዊው “የዛሬይቱ ኢትዮጵያ” ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በመሆን ለብዙ ጊዜያት ማገልገላቸው ተገልጿል፡፡
ደራሲና ጋዜጠኛው የተለያዩ መፃህፍትን ለንባብ ያበቁ ሲሆን ከእነሱም መካከል ታሪክ ጠቀሶቹ “ህግ ያልገዛውን ነፃነት ሃይል ይገዛዋል” እና “የኢትዮጵያ የታሪክ ጉዞ እስከቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ ዘመነ መንግስት” የሚሉት ይገኙባቸዋል፡፡
“የኦሾዊት ምስጢር” የተሰኘው የትርጉም ሥራና የፊልም ባለሙያው የበቀለ ወያ ታሪክ የሆነው “የትውልድ አርአያ”ም ከሚታወቁባቸው ሥራዎቻቸው መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ ደራሲና ጋዜጠኛ ሽፈራው መንገሻ የ3 ልጆች አባት ነበሩ፡፡

Published in ጥበብ

ደጃዝማች ግርማቸው ተክለሀዋርያት (ከደጃዝማችነቱም በላይ ደራሲ ናቸው) የግብርና ሚኒስትር በነበሩበት ወቅት ነው፡፡ ደጋግመው የሚያዩት አንድ ሰራተኛ አለ፡፡ ቢሮዋቸው ሆነው በመስኮት ያዩታል፣ ከሥራ ሲወጡ ያዩታል፣ ወደ ሥራ ሲገቡ ያዩታል፡፡ ሰው ሁሉ ቢሮው በተከተተበት ሰዓት ሰማይ - ጠቀስ ቁመቱን ይዞ ግቢው ውስጥ ይንጎራደዳል፡፡ አንዳንድ ጊዜ የግብርና ሰራተኛ ሁሉ የሚፈራውን የቢሮዋቸውን አንፃር እሱ ደፍሮ ይንጎራደድበታል፡፡
“ሥራ የለውም?” በማለት ልቦናቸው ውስጥ ያንጎራድዱት ጀመር፡፡ አውጥተው አልጠየቁም። ብቻ በስራ መካከል “አለ? የለም?” በሚል ቀና ብለው በአይናቸው ይፈልጉታል፡፡ ከእርዝመትና ከቅጥነት ብዛት ተቆልምሞ ያዩታል፡፡
“ይሄን ጀልጋጋ ምን ፈረደብኝ” ሳይሉ አልቀሩም።
አንድ ቀን ይሄ ሰው ቢሮአቸውን ከፍቶ ገባ፡፡ እንደተቆለመመ ሲያዩት ገረማቸው፡፡
“ምን ነበር?” አሉት ዝም ስላለ፡፡
“ክቡር ሆይ፣ የፃፍኩት መፅሐፍ አለ”
ደጃዝማቹ ገረማቸው፡፡ ትክ ብለው አዩትና፡-
“ኧከከከከ … ባለሙያ ኖርሃልና-- ግሩም! ግሩም!” አሉ፡፡
“ታዲያ ምን እንዳደርግልህ ትፈልጋለህ?”
“ለማሳተሚያ ገንዘብ አጥቼ ተቀምጧል፡፡”
“እና …”
“ማሳተሚያውን እርስዎ …”
“ቆይ ቆይ እስቲ፡፡ መጀመሪያ ላንብበውና የሚቀጥለው በሚቀጥለው ይሆናል፡፡”
አመጣላቸው …
… አነበቡት፡፡ ግራ ገባቸው፡፡ መያዣ መጨበጫ የለውም፡፡ ከአንዱ ወዳንዱ ይዘላል፡፡ ገፀ ባህሪው ተለዋዋጭ ነው፡፡ አንድ ወር ሙሉ ከታገሉት በኋላ ደራሲውን አስጠሩት፡፡ ተቆልምሞ ፊታቸው ቆመ፡፡
“ለመሆኑ የመፅሐፍህን ርዕስ ምን አልከው?” ሲሉ ጠየቁት፡፡
 እየተኩራራ፡- “መቼ ነው የምሞተው?” አላቸው፡፡
ደጃዝማች ግልፍ አላቸው፡-
“አሁን ባንተ ቤት እየኖርክ ነው፣ ጀልጋጋ! ውጣ ከዚህ፣ ጥፋ ከፉቴ!!” ብለው አባረሩት፡፡
አንዳንዴ …. እንደዛሬ ሁሉ በምናብ ቀበጥ ያደረገኝ ቀን ይሄንን ጀልጋጋ በሐሳቤ አመናትላለሁ። ምን ፅፎ ይሆን? በእርግጥ የፃፈው አይረባም ነበር? ወይስ ደጃዝማቹ ተለምዷዊውን የአፃፃፍ ስልት ሙጥኝ በማለታቸው ሳይረዱት ቀሩ? ደግሞም’ኮ “ርዕሱ” ወጣ ያለ ነው፡፡ “መቼ ነው የምሞተው?” ከግለሰብ መብሰክሰኪያነት አልፎ ለመፅሐፍ ርዕስ እና ጭብጥ  ይሆናል? ሲሆንስ እንዴት ነው? …
… የመፅሐፉ ርዕስ ብቻ ሳይሆን የሰውየው ፀባይም ያልተለመደ ነው፡፡ ህግና ደንብ የሚገዛው አይመስልም፤ ሲፈልግ የሚሰራ ካልፈለገ የሚተው አይነት ነው፡፡ ከቅርብ አለቃው እስከ ሚኒስትሩ ድረስ ከእነመኖራቸው መርሳት እንዴት ተቻለው? ግሳፄያቸው ሳያስበረግገው፣ ማስጠንቀቂያቸው ሳያባንነው እንዴት ቀረ? መስሪያ ቤት የሚያሳየው ጸባዩ የክት ነው? ኑሮውስ እንዴት ነው? ቤት ንብረቱ? ወዳጅ ጎረቤቱ? …
…አንድ ቆጭባራ ሰው የሚሰጠንን ቆጭባራ (Absurd) ሥራ ያጣን ሆኖ ይሰማኛል፡፡ በተለይ ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት ወዲህ የመጡ ደራሲያን ሥራቸው “ግርንቢጥ” የሆነው ከህይወታቸው በመቀዳቱ እንደሆነ ተረጋግጧል፡፡ ኢዩጂን ኢኦኔስኮ፣ ሳሙኤል ቤኬት፣ ፍራንዝ ካፍካ፣ አልበርት ካሙ … ከቆጭባራ ህይወታቸው ቆጭባራ ሥራ ያፈለቁ ቆጭባራ ደራሲዎች ናቸው፡፡
ኢዩጂን ኢኦኔስኮ “Rhinoceros” (አውራሪስ) የተሰኘ የሙሉ ሰዓት ድራማ አለው፡፡ በዚህ ድራማ ውስጥ ሰዎች ሁሉ ወደ አውራሪስነት ተለውጠው አንድ ቤተሰብ ብቻ ሰው እንደሆነ ይቀራል፡፡ የድራማው ግጭት እንደ ብዙሃኑ አውራሪስ እንሁን፣ አንሁን ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ ኢኦኔስኮ የብዙሃን ተፅዕኖ እንዲያርፍበት የማይፈቅድ፣ ብቻውን “ሰው” ሆኖ ለመቀጠል የወሰነ አይነት ሰው ነው፡፡ አኗኗሩ ፍፁም ብቸኝነት የተጠናወተው ከመሆኑ የተነሣ እንደ ድራማው “ሰው ሁሉ አውራሪስ ሆኖ አልቋል ብሎ የደመደመ ይመስላል” ይሉታል፡፡
የእኛ “ጀልጋጋ” እንዲህ የወሰነ ነበር ይሆን?
ሌላው “ቆጭባራ” ደራሲ ሳሙኤል ቤኬት ነው። ከጓደኞቹ  ጋር ሲኒማ አይቶ ሲመለስ ስለሲኒማው እያወራና እየተከራከረ ነበር፡፡ አንድ እንግዳ የሆነ ሰው ተቀላቅሏቸው ክርክሩን አሳብሮ ገባ፡፡ ከዚያም ጩቤ አውጥቶ ቤኬትን ወጋው፡፡ እሞት አፋፍ ደርሶ ከተመለሰ በኋላ ያንን እንግዳ ሰው የታሰረበት ድረስ ሄዶ ጠየቀው። “ለምን ወጋኸኝ?”
“ለምን እንደወጋሁህ እኔም አላውቀው” ሲል መለሰለት፡፡
ቤኬት ይሄን መነሻ አድርጎ “ቆጭባራ” ህይወትና “ቆጭባራ” ድርሰት ጀመረ፡፡ የመጀመሪያና ብቸኛ ልቦለዱ “Molloy” በዋና ገፀባህሪው ሥም የተሰየመ ነው፡፡ ሞሎይ ቁርጥ ቤኬትን ነው የሚሉ ሀያሲያን አሉ፡፡ አንዳንዶቹ አጋማሹን ከራሱ ቀድቷል ይላሉ። Edith Kern `Moran – Molloy the hero as Author” በሚል ርዕስ ዋናው ገፀባህርይ እና ደራሲው የሚመሳሰሉበትን ነጥብ ተንትና አስረድታለች፡፡
የእኛስ “ጀልጋጋ” ጨው አልባ ህይወቱን ስለቀዳ ይሆን ለደጃዝማች ግርማቸው አልጣፍጥ ያላቸው?
ሌላኛው ፈረንሳዊ ደራሲ አልበርት ካሙ እንዲሁ ግራ የሆነ ጠባይ ነበረው፡፡ ዘሩ ከፈለቀበት ፈረንሳይ ይልቅ ለተወለደባት አልጄሪያ በማድላት ከቅኝ ግዛትነት እንድትላቀቅ ይታገል ነበር፡፡ በዚህም ተከስሶ እስከመታሰር ደርሷል፡፡
ካሙ ይሄ ገጠመኙ ከውስጡ ሳይጠፋ እስከ ህይወቴ ፍፃሜ ቆይቷል፡፡ ደጋግሞም በተለያዩ ሥራዎቹ ውስጥ አንፀባርቆታል። በተለይ “The Stranger” እና “Outsider” ተብሎ ከፈረንሳይኛ ወደ እንግሊዘኛ በተመለሰ ስራው ላይ በሽሙጥ አንፀባርቆታል፡፡ ዋና ገፀባህሪው ሜርሳልት ስለአንድ ጎረቤቱ የሚተርክበት ቦታ አለ፡፡ ያ ጎረቤቱ ለስምንት አመታት ያልተለየው ውሻ አለው፡፡ እንግዲህ የፈረንሳይንና የአልጄሪያን ግንኙነት የሚመሰጥረው በዚህ ሽማግሌና ውሻው ግንኙነት ነው። ሚፍታ ዘለቀ ከተረጎመው ከዚህ ልቦለድ (“ባይተዋሩ”) ላይ ያንን ቦታ እንጥቀስ፡-
“…ሽማግሌው ጎረቤቱ ሳልማኖን አገኘሁት። ከውሻው ጋር ነው፡፡ ለስምንት አመታት አልተነጣጠሉም። የስፓኔል ዝርያ የሆነው አጫጭር እግሮች ያሉት ውሻው የቆዳ በሽታ አለበት፡፡ ፀጉሮቹን እንዳለ አርግፎ ቆዳውን በቡኒ የደም ቋጠሮ የሸፈነ ለምፅ የሚመስል ማንጌ የሚባል በሽታ መሰለኝ፡፡ በአንዲ ትንሽ ክፍል ለረጅም ጊዜ አብረው በመኖራቸው አንደኛው ሌላኛውን መምሰል ጀምሯል። ሽማግሌው ሳልማኖ ፊቱ ላይ ቀያይ የደም ቋጠሮዎች ሲኖሩት የተጥመለመለና ብን ያለ ቢጫ ፀጉር አለው፡፡ ውሻው ልክ እንደጌታው፣ አንገትና እግሮቹን ወደፊት ያሰገገና ለምቦጩን የጣለ ነው፡፡ ከአንድ ዝርያ የተገኙ ቢመስሉም አንዱ ሌላኛውን አምርሮ ይጠላል፡፡ በየዕለቱ ሁለት ጊዜ ቀን አምስትና ምሽት አስራ አንድ ሰዓት ንፋስ ለመቀበል ይወጣሉ፤ በስምንት ዓመት ውስጥ አንድም ቀን መንገድ ቀይረው አያውቁም። በሩደሊዮን አውራ ጎዳና ውሻው የታሰረበትን ገመድ እየመነጨቀ፣ ሳልማኖ ደግሞ ወደራሱ እየጎተተ ልታዩዋቸው ትችላላችሁ፡፡ እንዲህ ሲሆን ሽማግሌው ሲያንባርቅና ውሻውን ሲደበድበው ይታያል፡፡ ይሄኔ ውሻው እየለገመ ወደኋላ ይቀራል፡፡ ጎታች ሽማግሌው ይሆናል፡፡ ውሻው እንደገና ረስቶት ጎተታና ምንጨቃውን ሲጀምር ማንባረቁና ዱላው ይከተላል፡፡ ይህ ሲሆን እግረኛው መንገድ ላይ ይቆሙና ውሻው በፍርሃት፣ ሽማግሌው፣ በጥላቻ ይፋጠጣሉ፡፡ ሁሌም እንዲህ ነው የሚኖሩት። ውሻው መሽናት ሲፈልግ ሽማግሌው በቂ ጊዜ ሳይሰጠው ስለሚጎትተው ሽንቱን መንገድ ላይ እያንጠባጠበ ያልፋል …”
(ባይተዋሩ ከገፅ 27-28)
  ፈረንሳይና አልጄሪያ ለአልበርት ካሙ እንደ ሽማግሌውና ውሻው ናቸው፡፡ እየተጓተቱ፤ አልጄሪያ ለመመንጨቅ እየሞከረች፣ ፈረንሳይ እየቀጣችና እየተቆጣች አብረው አርጅተዋል፡፡ የሽማግሌውና የውሻው መጨረሻ የሁለቱ አገሮች መዳረሻ እንደሆነ ካሙ ያምናል፡፡ ውሻው ይጠፋል፣ ሽማግሌው ይናውዛል፡፡ ፀቡና መጓተቱ ሱስ ሆኖበት፣ ሌሊት ሌሎች ውሾ በጮሁ ቁጥር እየባተተ ቀሪ ህይወቱን ይገፋል፡፡
የእኛ “ጀልጋጋ” እንዴት ያለ መመስጠር፣ በእንዴት ያለ ሁኔታ ስራው ውስጥ አስገብቶ ነበር ይሆን?….
….ላልታተመ፣ እንደውም የት እንደገባ ለማይታወቅ መፅሐፍ (ምንም በምናብ ቀበጥ ቢያደርገኝ) ይሄን ያህል በሀሳብ መመናተል ተገቢ ነው? አይመስለኝም! ምክንያቱ ደግሞ ግልፅ ነው። የእኛ አንባቢዎች ወጣ ያሉ የጥበብ ስራዎችን በትከሻ ግፊያ ከማሽቀንጠር ጋብ ብለው ሲያቀርቡ ስለማይታይ ነው፡፡ ለምሳሌ፡- የዳንኤል ታዬ “ቅዠት” ከዚሁ ዘርፍ የሚመደብ ሥራ ቢሆንም ከአሥር አመታት በላይ የገበያ ደጅ እንዲጠና ተገድዶ ነበር። የዳዊት ፀጋዬ “ነጥቡ”ም እንደዚያው ከመገፍተሩ አልፎ ለደራሲው ስድብ አትርፎለት አልፏል፡፡ አሁን ደግሞ …
….አሁን ደግሞ የአልበርት ካሙ “The stranger” (Outsider) “ባይተዋሩ” በሚል ርዕስ በሚፍታ ዘለቀ ተተርጉሞ ቀርቦልናል፡፡ የካሙ ፍልስፍና መተርጎሚያ እና ማስተንተኛ የሆነው ይሄ ትልቅ ሥራ፤ እኛ ዘንድ ለመቀላቀል ሳይችል ቀርቶ ደጅ እንዲጠና የተፈረደበት ይመለስላል፡፡ የካሙ ሥራዎች በአማርኛ ተፈልገው አለመገኘታቸው ነውር ሆኖ ቆይቷል፡፡ ከዚያ በላይ ነውራችን ደግሞ ተተርጉሞ ሲቀርብ ፊት መንሳታችን ነው። የአንድ ቋንቋ ሥነ-ፅሑፍ አንገቱን መድፋት የሚገባው ይሄኔ ነው፡፡ እንኳን ሥም ያለው ብዙ የተባለለትና ከፍ ከፍ የተደረገ ደራሲ ቀርቶ ጀማሪውንም ቢሆን በቋንቋችን ጠልፈን የኛ ማድረግ የተገባ ነበር፡፡ ነገር ግን…፡፡  

Published in ጥበብ

     ለእርሻ አስፈላጊ የሆኑ ማዕድናት፣ በምግብና በኢንጂነሪንግ ጥበብ ዲዛይን አድርጎ ከፋብሪካ በሚሰራቸው ሸቀጦች አምራችነት በመላው ዓለም የሚታወቀው Israel Camical Limited (አይሲኤል) ኩባንያ በአፋር ክልል በፖታሽ ማዕድን ፍለጋ የተሰማራውን አላና ፖታሽ ኩባንያ መግዛቱን አስታወቀ፡፡
አይሲኤል ኩባንያ በሳምንቱ መጀመሪያ በቴልአቪቭ እስራኤል ባወጣው መግለጫ፤ በኢትዮጵያ በፖታሽ ምርት ልማት የተሰማራውን የካናዳውን የማዕድን ከባንያ አላና (“Allana”) በእጁ ማስገባቱን ጠቅሶ፣ ሽያጩም በካናዳ ጠቅላይ ፍ/ቤትና በአላና ኩባንያ የአክሲዮን ባለቤቶች መፅደቁን ገልጿል፡፡ አይሲኤል አላናን ንብረቱ ያደረገው ለ83.78 በመቶ ድርሻ 137 ሚሊዮን የካናዳ ዶላር በመክፈል ሲሆን ቀደም ሲል በ2013 ለ16.22 በመቶ የአላና ድርሻ 25 ሚሊዮን የካናዳ ዶላር ገዝቶ እንደነበር በመግለጫው ገልጿል፡፡
አላና በአፋር ክልል በደናክል አካባቢ የፖታሽ ማዕድን ለማውጣት ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ተዋውሎ እንደነበር የሚታቅ ሲሆን በ2013 ፌብሩዋሪ በተጠናቀቀው የአዋጪነት ጥናት መሰረት፣ ፕሮጀክቱ ለ25 ዓመታት በየዓመቱ እስከ አንድ ሚሊዮን ቶንስ ሙሪዬት ፖታሽ ማምረት የሚያስችል ክምችት እንዳለው ገልፆ እንደነበር መግለጫው አመልክቷል፡፡
አይሲኤል አላናን ሙሉ በሙሉ መረከቤ፣ በደናክል የማደርገውን የማዕድን ቁፋሮ ልማት ለማፋጠን ይረዳኛል ብሏል፡፡ በአሁኑ ወቅት የፕሮጀክቱን የቴክኒክና ትግበራ ጥናት የጀመረ ሲሆን ጥናቱም፣ ሎጀስቲክስ፣ መሰረተ ልማትና ለምርት አስፈላጊ የሆኑ ግብአቶች የደናክልን የፖታሽ ክምችት በሚገባ መጠቀም የሚቻልበትን ሂደት፣ ክምችቱ ያለበትን ስፍራ እንዴት ማሳደግ እንደሚቻልና አስተማማኝ የገንዘብ ምንጭ የሚገኝበትን መንገድ ያካትታል፡፡
በአገሪቷ ከፍተኛ የማዕድን ቁፋሮ ሲጀመር ለአጠቃላይ የአገሪቷ ጂዲፒ ዕድገት፣ ወደ አገር ለሚገባ የውጭ ምንዛሬ፣ ከታክስ ለሚገኝ ገቢ፣ በቀጥታ፣ ሆነ በተዘዋዋሪ ለአፋር አካባቢ የሚፈጠረውን የሥራ ዕድል… ለረዥም ጊዜ የሚያገለግል መሰረተ - ልማት ለኢኮኖሚው የሚያበረክተውን ጥቅም የኢትዮጵያ መንግስት እንደሚረዳ የጠቆመው አይሲኤል፣ በአፋር ክልል ለምንጀምረው መሰረተ ሰፊ የማዕድን ቁፋሮ የኢትዮጵያ መንግሥት ውሃ፣ መብራትና መንገድን ጨምሮ የተፈጥሮ ሀብትና መሰረተ ልማት ያሟላል የሚል እምነት አለን ብሏል፡፡  መሆኑን ማወቅ አለበት በማለት አስገንዝቧል፡፡
አይሲኤል የአክሲዮን ድርሻው በኒውዮርክና በቴልአቪቭ ስቶክ ኤክስቼንጅ አስመዝግቦ በመላው ዓለም፣ በእንግሊዝ፣ በስፔይን በእስራኤል፣ በኤስያ ገበያዎችና በአፍሪካ የሚንቀሳቀስ የቢዝነስ ኩባንያ ሲሆን፣ 12,500 ያህል ሰራተኞች እንዳሉት ይገመታል። ባለፈው ዓመት ከምርቶቹ ሽያጭ በአጠቃላይ 6.1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱ ታውቋል፡፡

Saturday, 27 June 2015 09:30

እድሳት እና ውሃ ልኮች

“Poor people were bad to each other, too – really bad to each other. My mother always says, if you are ugly the worst place to be ugly is around poor people. And what she means is that the people at the bottom always internalize the economy and are more deranged. We are likely to torture an ugly person than the people who taught us that we are ugly.”
Junot DIAZ


“አንድ ሰው የሰራው ቤት ያረጀ እንደሆነ ከመንገር ይልቅ ከጐኑ አዲስ ቤት ሰርተህ በማሳየት እንከኑን መግለፅ የተሻለ ነው” የሚል የአተያይ መንገድ አለ፡፡
እንግዲህ አሮጌው የሰውየው እውነተኛ ገፅታ ነው፡፡ ስለ አሮጌነቱ ወይንም አዲስነቱ ሰውየው የሚያውቅበት ማነፃፀሪያ አልነበረውም፡፡ ማነፃፀሪያ እንደማይፈልጉም አያውቅም ነበር፡፡ በቃ እራሱን መስሎ እና ሆኖ ህይወቱን እየገፋ ቆይቷል፡፡
ከዚህ በራሱ ማንነት ውስጥ ቅናት እና መንጠራራት ያልነበረው ሰው ጎን ሌላ ሰው መጥቶ … አዲስ ወይንም የተሻለ የተባለውን ቤት ቀለሰ፡፡
በመቀለሱ በአንድ ጊዜ ሁለት መለኪያዎችን ነው ያፀናው፡፡ አንደኛው መለኪያ “ውበት” ነው። ያለ ተቃርኖ ይኖር የነበረው የቀድሞው ሰው ቤት ጎን ውበትን ወይንም አዲስነትን የሰራው ሁለተኛው ሰው ውበትን ብቻ አይደለም የፈጠረው፡፡ በዚያው ቅፅበት አስቀያሚነትንም ፈጥሯል፡፡ አዲሱ ቤት ውበት እና አዲስነትን ይዞ ሲወለድ የቀድሞው ቤት አሮጌ እና አስቀያሚ መሆኑን መስክሯል፡፡
ከአሮጌው ቤት ጎን የተሰራው ቤት ይዞ የመጣውን ማንኛውንም እሴት ቀድሞ ቆሞ በቆየው ቤት ላይ እንዳልነበረ መስክሮበታል፡፡ በዚያ ቅፅበት የድሮው ቤት አሮጌ መሆኑ በአዲሱ ቤት ነፀብራቅ ውስጥ ይታያል፡፡ በመታየቱ ግጭት እና ተቃርኖ በቀድሞው አንድነት ፈንታ ይተካል፡፡ ይህ ተቃርኖን “abstraction” ብለው ምዕራባውያኑ ይጠሩታል። ምስራቃዊያኑ ደግሞ “መቼም መልሶ የማይገጥም የልዩነቶች መፈልፈያ የፓንዶራ ሳጥን ተከፍቶ ሰዎች ዝንተ አለም ወደ ማይስማሙበት መቀመቅ ከቷል” ይሉታል፡፡
አዲሱን ቤት የሰራው ሰው የውበትን እና የአስቀያሚነትን እውቀትም የሚያሳይ መስታወት ሰርቷል፡፡ በተራማጅ እና ኋላ ቀርነት መሀል ያለውን ክፍተት ፈጥሯል፡፡ የጥንቱ በአሮጌነቱ እንዲሸማቀቅ አዲሱ በጥንቱ ላይ እንዲሳለቅ ማድረጊያውን መስታወት ፈልስፏል፡፡
“መፍጠር መለየት ነው” የሚሉት እንዳሉ ሁሉ “መለየት መቃረን ነው” የሚሉም የዛኑ ያህል ማስረጃ አላቸው፡፡
እንግዲህ እነዚህ ሁለት አዋቂዎች አለምን ፈጥረዋታል፡፡ ወይንም አጥፍተዋታል፡፡ የውበትን ትርጉም በአዲሱ ቤቱ ላይ አስፍኛለሁ ብሎ የሰበከው ሰው ስብከቱ ተቀባይነት እስካገኘ ድረስ ብቻ የአሮጌውን ቤት አስቀያሚነት መመስከር ይችላል። ይህ ካልሆነ ግን፤ አዲሱም የተሻለ አይደለም .. አሮጌውም የባሰ  አይሆንም፡፡ አዲስ እና አሮጌ የሚፈጠሩት አዲስነት ከአሮጌነት የበለጠ ስለሆኑ የሚታወቅ ከሆነ ብቻ ነው፡፡
ማነፃፀሪያ ከሌለ ልዩነት የለም፡፡ የአውሮፓ ፍልስፍና ከምስራቅ ፍልስፍና ጎን ህንፃውን ገንብቶ አዲስ እና የተሻለ ስለመሆኑ (በጉልበቱ) ባያሳምን ሁለተኛም ሆነ ሶስተኛ አለም የሚባሉ የአስቀያሚነት ማረጋገጫዎች ባልተፈጠሩ ነበር፡፡
በዚህ የእይታ መነፅር ከተመለከትን አሪስጣጣሊስ አለም፣ (የምእራባውያን እውቀት) ውበት ከአፍሪካውያን በልጦ የኖረበት ምክኒያት ለመረዳት አያስቸግረንም፡፡
በልጦ መኖር ማለት አዲስነቱን፣ ውበትነቱን፣ እውነትነቱን በአሮጌዎቹ ጎን ሰርቶ እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ “ውበት ነኝ፤ እውነት ነኝ፤ እውቀት ነኝ” በማለት ብልጫውን ካፀናው ጎን የእሱ ተቃራኒ ይኖራል፡፡ አሮጌዎቹ፣ ኋላቀሮቹ አስቀያሚዎቹ፣ ደንቆሮዎቹ… ወዘተ፡፡
ከምዕራብ ጎን ምስራቅ አለ፡፡ ከአውሮፓ ጎን አፍሪካ፣ ከአሜሪካ ጎን ህንዶች …. ወዘተ፡፡ ውበትነቱን የሚያረጋግጠው ከአስቀያሚ ጎን በመቆም ነው፡፡ እውነትነቱን ያረጋገጠው በጉልበት ነው፤ አሮጌው ፅንሰ ሀሳብ ጎን አዲስ ፅንሰ ሃሳብ ገንብቶ አሮጌውን በማድከም፡፡ የደከመ ሁሉ አስቀያሚ ነው፡፡ የደከመ ሁሉ ኋላ ቀር ነው፡፡ ያዳከመ ሁሉ ደግሞ፣ አዲስ እና የተሻለ ስለመሆኑ ማረጋገጥ ይችላል። ስለዚህ የውበት ፅንስ ሲፈጠር በዚያው ቅፅበት የአስቀያሚነት ፅንሰ ሀሳብም ውሃ ልኩ ተቀምጧል፡፡
መስታወት የሚያሳየው (የሚያንፀባርቀው) ነገር ምንድነው? ካላችሁኝ፤ መልሴ ፅንሰ ሀሳብን ነው የሚል ይሆናል፡፡ ክርስቶስ ድህነትን በሰበከበት ዘመን ሀያል የነበሩት ሌሎች ናቸው፡፡ የእነ አሪስጣጣል ልጆች ያኔ መስታወቱን በአሪስጣጣሊስ ፊት ብትደቅኑት የእሱን መልክ የስልጣኔ፣ የአይሁዶቹን መልክ የወመኔ አድርጎ ይተረጉምላችሁ ነበር፡፡ እውነታው ሳይቀር ፅንሰ ሀሳቦች ተቀየሩ፡፡
የአሪስጣጣሊስ ወንበር ወድቆ የክርስቲያኖቹ ወንበር ተቃና፡፡ ውበትም በቀድሞው የሰውነት መስታወት ፊት ነፀብራቋ ተቀየረ፡፡ ድህነት ውበት እና እውነት ሆነ፤ ምክኒያታዊነት ደግሞ አሮጌው ቤት ሆነ፡፡ ሁለቱ ቤቶች ሁሌም ጎን ለጎን የቆሙ ናቸው። ዝንተ አለም አይነጣጠሉም፡፡ አንዱ ሌላውን ያስቀይማል፡፡ አንዱ በሌላው ድካም ተጠቅሞ ሀይሉን ያቋቁምበታል፡፡ ስለዚህ አፍሪካውያን ውብ መሆን የጀመሩለት እነማን በማስቀየማቸው ምክኒያት እንደሆነ ግልፅ ይሁንላችሁ፡፡ የሙስሊሞች መነቃቃት በነማን ማንቀላፋት እንደወጣ አይጥፋችሁ፡፡
አስቀያሚነታቸውን ማን ሰጥቶአቸው በልዋጭ የራሱን ውበት እንደፈለሰፈ እስኪገባቸው አስቀያሚዎች ስለራሳቸው አያውቁም፡፡ ይጨካከናሉ .. ውበታቸውን ያሸጣቸውን ለመምሰል ይጥራሉ። የንግስና ዘመኑ እስኪያበቃ፣ ለአስቀያሚዎቹም የውድቀት ጉድጓዳቸው የመውደቂያ ወለል ላይ አይደርሱም፡፡ አንዱ መውጣት መውጣት ብቻ … ሌላው መውደቅ መውደቅ ብቻ፡፡ … ይህ የውድቀት እና የኃያልነት ተቃራኒ ስፍራቸው ዘላለማዊ እስኪመስል ድረስ ለሺ አመታት ሊቀጥል ይችላል፡፡ ግን በስተመጨረሻ መቀየሪያው ይደርሳል፡፡
ቅድም መፃፍ ስጀምር … አዲስ ቤት ከአሮጌው ቤት ጎን ስለሰራው ሰው ያወራሁላችሁ ለመረዳት እንዲቀላችሁ ብዬ ነው፡፡ በመሰረቱ አዲስም አሮጌም ቤት የለም፡፡ ሁለቱም ቤቶች ከጥንት ጀምሮ ያሉ ናቸው፡፡ አዲስ ቤት የሰራ የመሰለንም ሰው ቤቱን አዲስ አስመስሎ ስላደሰው እንጂ በመሰረቱ አዲስ ነገር “ከሰማይ በታች የለም”። አንደኛው አዲስ አስመስሎ የቀድሞውን ቤት በአዲስ የፅንሰ ሀሳብ ይዘት ሳይሆን ቅርፅ ሲያድሰው … በተቃራኒው ያለው ቤት ባለመታደሱ አሮጌ መስሎ መቅረቱ … የእውነት እና ውሸትን ያህል ልዩነት ያላቸው አስመስሎ አለያያቸው እንጂ በመሰረቱ አንድ ናቸው፡፡
አስቀያሚ ያስመስላቸውም ሆነ ውብ ያደረጋቸው የሀሊዮት መስታወት እንጂ ጉልበታቸው እና ባለጊዜነታቸው የሚለዋወጥ ነው፡፡ ፀንቶ የሚኖር ማንነታቸው፣ ልዩነታቸውን ወደ አንድነት አይቀይርላቸውም፡፡ ከሁለቱ ቤቶች በላይ የሆነ ሦስተኛ እና ሁለቱን አንድ የሚያደርጋቸው ቤትም መቼም አይቀልሱም፡፡

Published in ጥበብ

በዓለም ዝምና ዝናቸው የገነነ፣ ምርጥ ባለ 5 እና 4 ኮከብ ሆቴሎች ቢኖሩም በአፍሪካ ስለሌሉ ብዙም አይታወቁም፡፡ በአፍሪካ የሌሉት ደግሞ በአጋጣሚ አይደለም - ሆን ብለው ነው፡፡ እንግዲህ የሆቴል ቢዝነስ ትርፍ ላይ ያተኮረ አይደል! አብዛኛው የአፍሪካ ህዝብ ድሃ ስለሆነ ሆቴሎቹ ቢሰሩም ተጠቃሚ አይኖራቸውም በማለት ነው፡፡
አሁን ግን ሁኔታዎች እየተለወጡ ነው፡፡ ብዙ የአሜሪካና የአውሮፓ አገሮች ኢኮኖሚያቸው ክፉኛ ዳሽቆ ከዚያ ማጥ ውስጥ ለመውጣት ሲዳክሩ፣ ብዙ የአፍሪካ አገሮች የለውጥና የዕድገት ጎዳናውን ተያይዘውታል። ጥቂት አገሮችም በዘመናት ከሚታወቁበት ድህነት አፈትልከው መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች ተርታ ለመሰለፍ ቀን ቆርጠዋል፡፡ ለዚህ ነው እንግዲህ ታዋቂዎቹ የዓለም ሆቴሎች ፊታቸውን ወደ አፍሪካ ያዞሩት፡፡ ካርልሰን ሬዚዶር፣ ስታር ውድ፣ ማንጋሊስ፣ ሮታና፣ ሉቨር ሆቴል ግሩፕ በሚሉ በሚታወቁና ሌሎችም ወደ አፍሪካ እየተመሙ ነው፡፡
መቀመጫውን ሌጎስ ናይጄሪያ ያደረገው ደብሊው ሆስፒታሊቲ ግሩፕ የተሰኘ አማካሪ ድርጅት ይፋ ባደረገው የዘንድሮ ዓመት ሪፖርት፤ ወደ አፍሪካ ለመግባት እየተወዳደሩ ያሉትን 10 ከፍተኛ ሆቴሎች ዝርዝር አውጥቷል፡፡ በአፍሪካ 7,250 ክፍሎች ያላቸው አዳዲስ ሆቴሎችን ለመገንባት ዝግጅቱን ጨርሶ ፉክክሩን እየመራ ያለው ሂልተን ሆቴል ሲሆን ከዚህ ውስጥ 18 በመቶዎቹ ባለፈው ዓመት የተጀመሩ ናቸው ተብሏል፡፡   
6,953 ክፍሎች ያላቸውን 32 አዲስ ሆቴሎች በመገንባት አፍሪካን ለማልማት 2ኛ ሆኖ እየገሰገሰ ያለው ካርልሰን ሬዚዶር ነው፡፡ በ3ኛ ደረጃ እየተከተለ ያለው ደግሞ ማርዮት ነው፡፡ 6, 412 ክፍሎ ያላቸውን 36 አዳዲስ ሆቴሎች ሊጀምር ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ 22 በመቶዎቹ ባለፈው ዓመት የተጀመሩ ናቸው።
በአዳዲስ ሆቴሎች ግንባታ ደግሞ 36 ሆቴሎችን በመገንባት ላይ የሚገኘው ማሪዮት ቀዳሚ ነው። 32 እና 29 አዳዲስ ሆቴሎች በመገንባት ካርሊሰን ሬዚዶር 2ኛ፣ ሂልተን 3ኛ በመሆን ይከተላሉ፡፡ ወደ አፍሪካ ገበያ ከገቡትና በመግባት ላይ ካሉት ሆቴሎች መካከል በአዳዲስ ሆቴሎች ግንባታና በክፍሎች ብዛት የመጀመሪያዎቹን 10 ምርጥ ሆቴሎች ከዚህ በታች ይመልከቱ፡፡

Page 2 of 16