ግንቦት 9 ቀን 2006 ዓ.ም በወጣው የጋዜጣችሁ ዕትም፣ ጤና ዓምድ ላይ “የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች በአሳሳቢ ደረጃ ላይ ናቸው ተባለ” በሚል ርዕስ ያወጣችሁትን ዘገባ የኢትዮጵያ የጥርስ ህክምና ባለሙያዎች ማህበር ተመልክቶታል፡፡
በጥርስ ህክምናም ሆነ በየትኛውም የህክምና ዘርፍ ያሉ ጉድለቶችን በማሳየት እርምት እንዲደረግና ህብረተሰቡ ተገቢውን ህክምና እንዲያገኝ ማሳሰባችሁ አግባብነት ያለው ነው፡፡ ሆኖም የሰራችሁት ዘገባ ማህበረሰቡን ፍርሀት ውስጥ የሚከትና የተሳሳት መረጃ የሚሰጥ  ሆኖ አግኝተነዋል፡፡
ከሁሉም በላይ በማንኛውም ዜጋ ላይ እንዲደርስ የማንመኘው ችግር የደረሰባት እህታችን፤ የኛም ጉዳይ ነችና ህመሟ ይሰማናል፤ ችግሯም ይመለከተናል፡፡ ነገር ግን ባለሙያ ያልሆኑ ጥቂት ሰዎች በሚሰሩት የተሳሳተ ስራ /በእርግጥ የተባለው ታሪክ ከተከሰተ/ ምክንያት “አብዛኞቹ ክሊኒኮች” ተብሎ መዘገቡ በእጅጉ ያሳምማል፡፡
ለመሆኑ አንድ የጥርስ ህክምና ክሊኒክ ለመክፈት የሚያስፈልገውን መስፈርት አንብባችሁታል? ታዲያ ያን ሁሉ ገንዘብ አፍስሶ፣ የተሳሳተ ስራ በመስራት የሚደሰት ባለሙያ ይኖራል? ለመሆኑ የህክምና መሳሪያዎችን መቀቀያ ማሽን ዋጋው ስንት ነው? ደግሞስ ሃኪሙ ምን ያህል ሞኝ ቢሆን ነው በአግባቡ ንፅህናው ባልተጠበቀ መሳሪያ እየሰራ ከታካሚውም በላይ እራሱን ለበሽታ የሚያጋልጠው? እውነት እናውራ ከተባለ አይመስልም!!!
ዘገባውን የሰሩት ጋዜጠኛስ መሳሪያዎቹን “አየሁ አላየሁም” የሚሉት፣ ስለህክምና መሳሪያዎቹ እውቀት ኖሯቸው ነው ወይስ የነገሯቸውን ብቻ ይዘው ነው? መቼም ስለሚሰሩት ዘገባ መረጃ ቀድሞ መጠየቅ ግዴታ ይመስለናል፡፡ በእርግጥ ዕውቀቱ፣ ችሎታውና ልምዱ የሌለው በልምድ የሚሰራ ተራ ግለሰብ የህክምና ስህተት ሰራ ቢባል ያስኬዳል፡፡ ባለሙያ ያልሆነ ሰው ምን እንደሰራና ምን እንዳጠፋ ለይቶ አያውቅምና፡፡ እንዲህ ያለው ዘገባ፣ በአሁኑ ሰዓት የህክምና ባለሙያዎች ማህበረሰቡን በምን አይነት ሁኔታ ውስጥ ሆነው እያገለገሉ እንዳሉ ካለመረዳት ወይም ለመረዳት ካለመፈለግ የመነጨ በመሆኑ ማዘናችንን እንገልፃለን፡፡
የእህታችን ታሪክ የተገለፀበት መንገድና የተብራሩት ችግሮችን ለመተቸት እውነተኛውን ታሪክ ማግኘትና መገምገም ይጠበቅብናል፡፡ ሳናነሳ የማናልፈው ግን የጥርስ ህክምና ለመስጠት የሚችሉ የተለያዩ ባለሙያዎች መኖራቸውን እንድታወቁ ሲሆን ዘገባው የሚገልፀው አይነት የጥርስ አካል አለመኖሩንና በተጠቀሰው ሆስፒታል ውስጥ የጥርስ ህክምና ክፍል እንደሌለ እንዲሁም የጥርስ ሀኪም አለመኖራቸውን ነው፡፡ አስተያየት ሰጥተዋል የተባሉት የጥርስ ሀኪምም የማህበሩ አባል አይደሉም፡፡ በዘርፉ የተሰማሩ ባለሙያዎችን ጠይቀንም የሚያውቃቸው አንድም ሰው አላገኘንም፡፡ ከአንድ ባለሙያም ይህን አይነት አስተያየት እንደማይሰጥ ስለምናምን፣ የዘገባው አላማ ሌላ ሊሆን እንደሚችል ገምተናል፡፡
ህብረተሰቡ ተገቢውን ህክምና እንዲያገኝ ማድረግ፤ ባለሙያውም ተገቢውን ስራ በተማረበት መስክ እንዲፈጽም ግዴታዎቹን በአግባቡ ተወጥቶ፣ መብቱም እንዲከበርለት መስራት የተቋቋምንበት ዋና ዓላማችን ነው፡፡ ለዚህም ሚዲያው ያለው ድርሻ ጉልህ መሆኑን ከልባችን እናምናለን፡፡ ነገር ግን የአገሪቱን አቅምና የባለሙያውን ሁኔታ ባለማጤን “አብዛኞቹ” ክሊኒኮች በሚል የወጣው ዘገባ፤ ለህብረተሰቡ የተሳሳተ መረጃ በማድረስ፣ ሥራችንን ካለውም በላይ ከባድና ውስብስብ ስለሚያደርግብን እባካችሁ በጥንቃቄ ዘግቡ እንላለን፡፡ በተረፈ ማናቸውንም መረጃዎች ለመስጠትና በዘርፉ ለሚከሰቱ ችግሮች አፋጣኝ የመፍትሔ እርምጃ ለመውሰድና በትብብር ለመስራት ፈቃደኞች መሆናችንን እንገልፃለን፡፡  

Published in ጥበብ

    “በሬዲዮ ድራማና ሙዚቃ የምናውቃቸውን እነ እሙዬን፣ እነ ሚሚን… በአካል በማየታችን በጣም ተደስተናል፤ በጣም ነው የምንወዳቸው’ኮ”
“እነዚህ ሴት ልጆች በራዲዮ ድራማና ሙዚቃ የሚያስተላልፉት መልእክት ቀላል እንዳይመስልህ። እኔማ፣ ምነው ቀደም ባሉ ነው ያልኩት፡፡ በልማዳዊ ጎጂ ባህል ተሽብቤ ሁለቱን ሴት ልጆቼን ለጥቃት መዳረጌ፣ አሁን በጣም እየቆጨኝ ነው። ላለፈ ክረምት… እንዲሉ ሆነ እንጂ ለትናንሾቹማ ደርሻለሁ።…”
ያለዕድሜ ጋብቻና እርግዝና፣ ት/ቤት አለማግባት፣ ሳያጠናቅቁ መውጣት፣ የፆታ ጥቃትና ትንኮሳ… በሴት ልጆች ላይ ከሚፈፀሙ ጎጂና ልማዳዊ ድርጊቶች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ እነዚህ ጐጂ ድርጊቶች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየተሻሻሉ ቢሆንም አሁንም ድረስ በመላ አገሪቷ የተንሰራፉ ሰንኮፎች ናቸው፡፡ ድርጊቱ ደግሞ በአማራ ክልል ይብሳል፡፡ ለዚህ ነው፣ “የእኛ”፣ “ድምፃችን ይሰማል!” የተሰኘው ፕሮጀክት፣ ኅብረተሰብ ለሴት ልጅ ያለውን ግንዛቤ እንዲለውጥ የሙከራ የራዲዮ ድራማና ሙዚቃዊ ትምህርት በዚሁ ክልል የጀመረው፡፡
የእኛ የድራማና የሙዚቃ ባንድ በአምስት ሴቶች የሙከራ ስራውን ከጀመረ አንድ ዓመት ሆኖታል፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ በሸገር፣ በአማራ ራዲዮ፣ በደሴ፣ በባህርዳርና በደብረብርሃን ኤፍ ኤሞች ሲያስተላልፍ የቆየውን ሁለት ክፍል የራዲዮ ድራማ አብቅቶ ሦስተኛውን ክፍል ባለፈው እሁድ ጀምሯል፡፡
የሁለተኛውን ክፍል ድራማ ማብቃትና የሦስተኛውን መጀመር ለማብሰር አምስቱ አርቲስቶች በ11 የአማራ ክልል ከተሞች ያቀረቡት የሙዚቃ ኮንሰርት ያበቃው፣ በጎርበላና በደብረብርሃን ከተሞች ነበር፡፡ ጎርበላ፣ የአንኮበር ወረዳ ዋና ከተማ ስትሆን መጠሪዋን ያገኘችው ከወራሪው የኢጣሊያ ጦር ነው፡፡ ጎርቤላ በጣሊያንኛ “የልቤ ፋና፣ የልቤ ቆንጆ” ማለት እንደሆነ የከተማዋ ነዋሪዎች አጫውተውናል፡፡
አምስቱ ሴቶች በጎርቤላ ከተማ ያቀረቡትን የሙዚቃ ኮንሰርት ለመታደም፣ የከተማዋ ነዋሪዎች ብቻ ሳይሆኑ፣ ከሩቅ የገጠር ቀበሌዎች በሰልፍ የመጡ ሴት አርሶ አደሮችም ነበሩ፡፡ አርሶ አደር ሴቶች የመጡት፣ የአምስቱን ሴቶች “የእኛ” ሙዚቃ እየዘፈኑ ነበር፡፡ የኮንሰርቱ ተሳታፊዎች አርሶ አደር ሴቶችና ተማሪዎች ብቻ አልነበሩም፡፡ በራዲዮ የሚያውቋቸውን አምስቱን ሴቶች በአካል ለማየትና ደስታቸውን ለመግለጽ፣ ወጣቶችና አረጋውያን ሳይቀሩ ታድመዋል፡፡ ነዋሪው ሴቶቹ ሲጫወቱ አብሯቸው እየዘፈነ፣ እስክስታ ይመታና ይደንስ ነበር፡፡   
ወ/ሮ ሽታዬ ዓለምነው የ6 ልጆች እናት ናቸው። ጠጋ አልኳቸውና ከድራማና ከሙዚቃው ምን አገኙ? ስል ጠየቅኋቸው፡፡ “እኛ የሴቶች ማኅበር ስላለን በዚያ በኩል ድራማውን እንከታተላለን። ከዚያ በኋላ አንድ ለአምስት ተደራጅተን የለ? ጠርናፊያችን ትሰበስበንና በሰማነው ድራማ ላይ እንወያያለን፡፡ ሁላችንም የተሰማንን ሀሳብ ከተናገርን በኋላ፣ ትምህርቱን ያገኘችው ኃላፊ እንዲህ ነው እንዲህ ነው ብላ ታስረዳለች፡፡ በዚህ ዓይነት ብዙ ትምህርት አግኝተናል፡፡
ዓይኔ የበራው አሁን ስለሆነ ቀደም ሲል እንዲህ ዓይነት እውቀት ያለማግኘቴ ቆጭቶኛል፡፡ ያለፈው አለፈ፣ ምንም አይደረግም፡፡ ከአሁን በኋላ ግን ሴቶችም መብት እንዳላቸው ተረድቻለሁ፡፡…” አሉኝ፡፡ በደብረብርሃን ከተማም የነበረው ሁኔታ ተመሳሳይ ነው፡፡ የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች፣ ወጣት ሴቶችና ወንዶች፣ … በብዛት ተገኝተው ነበር፡፡ እዚህ ከጎረቤላው የሚለየው፣ በርካታ ታዳሚዎች፣ እየጨፈሩና እየደነሱ ዘፋኞቹን ሴቶች ያለማጀባቸው ነው፡፡
የ“እኛ” ፕሮግራም ከአማራ የትምህርት መገናኛ ማዕከል ጋር በመተባበር እየሰራ ሲሆን፣ ድራማው በሳምንት ሁለት ጊዜ በክልሉ በሚገኙ 8,000 ት/ቤቶች እንደሚተላለፍ፣ በምሥራቅና ምዕራብ ጎጃም የሚገኙ 200 ት/ቤቶች “የእኛ ክለብ” መስርተው በድራማው ላይ እንደሚወያዩ የፕሮግራሙ አስተባባሪዎች ገልፀዋል። ከዚህም በተጨማሪ ሩቅ በሆኑ አካባቢዎች ከአማራ ሴቶች ማኅበር ጋር በመተባበር የአድማጮችን ቁጥር እያበዛ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
“የእኛ” ፕሮግራም በ56 ወረዳና በስደስት ዞኖች፣ በምስራቅና ምዕራብ ጎጃም፣ በአዊ፣ በሰሜን ጎንደር፣ በደቡብ ወሎና ሰሜን ሸዋ ከሚሊዮን በላይ አባላት ያላቸው 42,000 ክበባት ለማቋቋም እየሰራ መሆኑ ተገልጿል፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 14 June 2014 12:28

ትንሿ የኮንሶ ዕንቁ

“ሙዚቃና ዳንስ ብወድም ትምህርቴን አልረሳም”

ገና የ8 ዓመት ህፃን ናት፡፡ ከኮንሶ ሙዚቃ ክሊፖች ላይ ጠፍታ አታውቅም፡፡ በኮንሶ ባህላዊ አለባበስ ደምቃ የኮንሶን ባህላዊ ጭፈራ ስታስነካው አይን ታፈዛለች፡፡ መልካምነሽ የአንደኛ ክፍል ተማሪ ስትሆን የኮንሶ ሁለተኛ አመታዊ የባህል ፊስቲቫልን ለመታደም ኮንሶ በነበርኩ ጊዜ አገኘኋትና “ለመሆኑ ጭፈራ እንዴት ለመድሽ?” አልኳት “አባቴን ኋላ ኋላ እየተከተልኩ እሱ ለፈረንጆች ሲጨፍር ተለማመድኩኝ” በማለት በኮልታፋና ጣፋጭ አንደበቷ መለሰችልኝ፡፡
በወረዳው የባህል ቡድን ውስጥ ተካትታ ከትምህርቷ ጎን ለጎን የሙዚቃ ተሰጥኦዋን እያጎለበተች የምትገኘው ህፃን መልካምነሽ፤ አባቷ እንደሚያበረታታትም ትናገራለች፡፡ ህፃኗ በአሁኑ ሰዓት በኮንሶ ሙዚቃዎች፣ በባህል ፌስቲቫሎችና መሰል ዝግጅቶች የባህል ቡድኑን እየመራች ያንን አፍዝ አደንግዝ ጭፈራዋን ማስነካት ለምዳዋለች፡፡ “የሚወጣ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል” እንዲሉ፣ ህፃኗ ነገ ለከፍተኛ ደረጃ እንደምትበቃ አያያዟ ያስታውቃል፡፡
አባቷ አቶ መሳይ ጌሌቦ፤ በልጅነቱ ወላጆቹን በሞት አጥቶ በሊስትሮነት ሙያ ልጅነቱን ሲገፋ የሙዚቃ ፍላጎት አድሮበት በውዝዋዜ ሙያ መግፋቱንና ትምህርቱን እስከ 12ኛ ክፍል ከተማረ በኋላም በጮራ ፀረ ኤችአይኢ ኤድስ ክበብ ውስጥ በውዝዋዜና በድራማ ብዙ እንደተሳተፈ ይናገራል። ሁለተኛ ልጁ መልካምነሽ ነፍሷ ወደ ጥበቡ ማድላቱን ሲገነዘብ ከማበረታታት ውጭ ምንም ተፅዕኖ እንዳላደርግባት የተናገረው አቶ መሳይ፤ “ፍላጎቷን አፍኜ እኔ በመረጥኩት መንገድ እንድትሄድ ባደርጋት ውጤታማ ልትሆን አትችልም” ብሏል። “ባይሆን በሙዚቃው ተስባ በትምህርቷ ላይ ቸልተኛ እንዳትሆን አግዛታለሁ” ባይ ነው፡፡  
ህፃኗ በሁለተኛው የኮንሶ የባህል ፌስቲቫል ላይ በተደረገው የጎዳና ላይ ትዕይንት የባህል ቡድኑን ከኋላ አስከትላ በባህላዊ ጭፈራዋ አጃኢብ አሰኝታለች፡፡
“አንዳንድ ጊዜ ዝግጅት ሲኖር ጋሞሌ እና ፋሻ የተባለ ራቅ ያለ ቦታ ሄደው ይለማመዳሉ፤ ያኔ እፈቅድላታለሁ” ያለው አባቷ፣ ይህቺ ልጅ እኔን ተከትላ ወደ ጥበቡ የገባች በመሆኑ ስሜቷን በትክክል በመረዳት አስፈላጊውን እገዛ ከማድረግ ወደ ኋላ አልልም ብሏል፡፡ ወደፊት ታዋቂ ሙዚቀኛ መሆን እንደምትፈልግ፣ አሁንም ቢሆን የኮንሶ ሙዚቃ ተጫዋቾች ሁሉ ክሊፕ ሲሰሩ እንደሚጋብዟት የገለፀችው ህፃኗ፤ በኮንሶ ካሉ የባህል ተወዛዋዦች ትንሿ ታዋቂ አርቲስት እንደሆነች አጫውታኛለች፡፡
“ጎበዝ ተማሪ ነሽ ወይስ በውዝዋዜ ብቻ ነው ጉብዝናሽ?” በሚል ላቀረብኩላት ጥያቄም፤ “በጣም ጎበዝ ተማሪ ነኝ፤ አባቴን ጠይቂው፤ ሙዚቃና ዳንስ ብወድም ትምህርቴን አልረሳም” ስትል ትንሿ ጥቁር እንቁ እየተፍለቀለቀች ነግራኛለች። “አንቺ ግን በቴሌቪዥን አይተሽኝ አታውቂም?” አለችኝ ድንገት፣ “አውቅሻለሁ ግን በተለይ በአካል ስትጨፍሪ ሳይሽ በጣም ደስ ትያለሽ” አልኳት፡፡ “የማትችይ ከሆነ አለማምድሻለሁ፤ ቀላል እኮ ነው” አለችኝ፡፡
መልካምነሽ ስለሙዚቃ ከማውራት ይልቅ በድርጊትና በጭፈራ ስሜቷን መግለፅ እንደምትወድ የሚናገረው አባቷ፤ ከመጀመሪያ ልጁ የተለየ ባህሪና ሁኔታ እንዳላት አጫውቶኛል፡፡ ታላቅ እህቷ የስድስተኛ ክፍል ተማሪና ግርግር የማትወድ ናት ያለው አቶ መሳይ፤ እሷን ብትሆን በትምህርቷ እንዳትሰንፍ ከማበረታት ውጭ በፍላጎቷ ጣልቃ ገብታ አትጨፍሪ ወይም እንዲህ አታድርጊ እንደማትላት ይናገራል፡፡
“ዝም ብዬ ሳስብ መልካምነሽ እንደ ሙዚቃ ፍላጎቷና ችሎታዋ፣ ኮንሶን ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያንም የምታስጠራ ይመስለኛል” የሚለው አባቷ፤ ገና ከአሁኑ አድናቂዋ እየበዛ፣ መምጣቱንም ጨምሮ ገልጿል፡፡ ትምህርትሽን ስትጨርሺ ምን መሆን ትፈልጊያለሽ አልኳት፤ “ታዋቂ ሙዚቀኛ መሆን እፈልጋለሁ” ነበር መልሷ፡፡
በፌስቲቫሉ የመዝጊያ ስነ-ስርዓት ላይ በዲላ ኮሴ ሆቴል ቴራስ ላይ በተደረገልን የእራት ግብዣ ወቅት፤ መልካምነሽ ከባህል ቡድኑ ጋር በማራኪ ጭፈራዋ ስታዝናናን አምሽታለች፡፡ ትኩረቱን በቱሪዝም ላይ አድርጎ የሚሰራው ሀገሬ ሚዲያና ኮሚዩኒኬሽን በቅርቡ በሚያሳትመው የፌስቲቫል ዳይሬክተሪ ላይ ፎቶዋን ሽፋን አድርጎ እንደሚያወጣ የገለፀ ሲሆን የመልካምነሽ አባት በዚህ የተሰማውን ደስታ ለመግለፅ ቃላት አጥሮት ነበር፡፡ “ልጄ በዚህ መልኩ የተለያዩ ድጋፎችና ማበረታቻዎችን ካገኘች አሁንም ትልቅ ደረጃ እንደምትደርስ አልጠራጠርም” ሲል ምስጋናውን ገልጿል፡፡ በሽፋንነት ለሚያወጣው የህፃኗ ፎቶ ክፍያ ይከፍላት እንደሆነ የጠየቅነው የሀገሬ ሚዲያና ኮሚዩኒኬሽን ባለቤት አቶ ሄኖክ ስዩም በበኩሉ፤ “ፎቶውን በሽፋንነት የምንጠቀመው ህፃኗን የበለጠ ለማበረታታትና ህዝቡ በደንብ እንዲያውቃት ለማድረግ ነው” ብሏል፡፡     

Published in ጥበብ

በሰዓሊና ረዳት ፕሮፌሰር ጌታቸው ዮሴፍ ህይወት ዙሪያ የሚያጠነጥነው “Love and Peace” መፅሀፍ የፊታችን ሐሙስ ከቀኑ በ9 ሰዓት በካፒታል ሆቴል ይመረቃል፡፡ በ72 ገፆች የተቀነበበው መፅሐፍ፤ በ150 ብር ለገበያ ይቀርባል ተብሏል፡፡ የተባባሪ ፕሮፌሰሩን የህይወት ታሪክ ፍንትው አድርጎ እንደሚገልፅ የተነገረለት መፅሀፉ፤ በስዊዘርላንዳዊቷ ኤልዛቤት ቢያሲዮ እና በአቶ ዮናስ ታረቀኝ የተዘጋጀ እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል፡፡
በሌላ በኩል የተባባሪ ፕሮፌሰር ጌታቸው ዮሴፍ አዳዲስ የስዕል ስራዎች የሚቀርቡበት የስዕል ኤግዚቢሽን በመጪው ማክሰኞ በላፍቶ አርት ጋለሪ የሚከፈት ሲሆን ለአንድ ወር ለተመልካች ክፍት ሆኖ እንደሚቆይም ተጠቁሟል፡፡    

“የዮድ አቢሲኒያዋ እመቤት” የሚል ቅፅል ስም በተሰጣት የባህል ዘፋኝ እመቤት ነጋሲ የተዘጋጀው “ሰንደዓ በል” የተሰኘ የሙዚቃ አልበም ባለፈው እሁድ በዮድ አቢሲኒያ የባህል ምግብ አዳራሽ ተመርቋል። አልበሙን ለማዘጋጀት ከ250ሺህ ብር በላይ እንደወጣበትም ተገልጿል፡፡
ድምፃዊ ፀጋዬ እሸቱን ጨምሮ በርካታ አርቲስቶች በተገኙበት የተመረቀው አልበሙ፤ በዕለቱ ለታዳሚዎች በሽያጭ ቀርቧል፡፡
ድምፃዊቷ በዮድ አቢሲኒያ የባህል ምግብ ቤት አዳራሽ ለስምንት አመታት የሰራች ሲሆን ዮድ አቢሲኒያን በመወከል በውጭ አገራት አምስት ስራዎቿንና ባህሏን አስተዋውቃ መመለሷም ተገልጿል። “ሰንደዓ በል” የተሰኘው የአልበሙ መጠሪያ የሙዚቃ ቪዲዮ የተሰራለት ሲሆን ወደፊት ለሁሉም ዘፈኖች ክሊፕ እንደምትሰራ ድምፃዊቷ በምረቃው ላይ ገልፃለች፡፡ ድምፃዊቷ የፈረመችበት አንድ ሲዲም ለጨረታ ቀርቦ አንድ የምሽቱ ታዳሚ በ6500 ብር አሸንፎ እንደወሰደው ታውቋል፡፡

የገጣሚ ኤፍሬም ስዩም ውርስ ትርጉም በሆነው “ተዋናይ” የተሰኘ የቅኔ መፅሃፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በብሄራዊ ቤተ መፃህፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ውይይት እንደሚካሄድ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ አስታወቀ፡፡
ለአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቋንቋና የስነፅሁፍ መምህር አቶ ይኩኖ አምላክ መዝገቡ፤ ለውይይቱ መነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡ ሲሆን የሥነፅሁፍ ቤተሰቦች በውይይቱ ላይ እንዲታደሙ ሙዩዚክ ሜይዴይ ጋብዟል፡፡

 የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቴአትር ጥበባት ትምህርት ቤት የሁለተኛ አመት የቀን ተማሪዎች፤ የአርሲ ባህል በሆነው የ “ስንቂ” ትውፊት ላይ ጥልቅ ምርምርና ጥናት በማድረግ፣ ባህሉን ወደ ድራማ ቀይረው ለእይታ ሊያበቁት እንደሆነ ተገለፀ፡፡ ይኸው ትውፊታዊ ድራማ ዛሬ ከምሽቱ 12 ሰዓት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አምስት ኪሎ አዳራሽ ለተመልካች ይቀርባል ተብሏል፡፡

የሩሲያ የሳይንስና የባህል ማዕከል ከጀርመን የባህል ተቋም ጋር በመተባበር፣ ከመቶ አመት በፊት የተነሱ የአዲስ አበባ ፎቶግራፎችን ለአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም በስጦታ አበረከተ፡፡ ፎቶግራፎቹ ከመቶ አመት በፊት ለህክምና አገልግሎት ወደ ኢትዮጵያ በመጡ ሩሲያዊ ሀኪም እንደተነሱ የተገለፀ ሲሆን የዚያን ጊዜውን የአዲስ አበባና ነዋሪዎቿን የህይወት ገፅታ አጉልተው እንደሚያሳዩም ተጠቁሟል፡፡
ፎቶግራፎቹ በሩሲያ ሴንት ፒተርቡርግ በሚገኘውና በታላቁ ንጉስ ጴጥሮስ ስም በተሰየመው እውቁ የኩንስትካሜራ ሙዚየም ባለቤትነት ተመዝግበው የሚገኙ ሲሆን ይህን ታሪካዊ የፎቶግራፍ ስብስብ አዲስ አበባ የሚገኘው የጀርመን የባህል ተቋም ከሙዚየሙ ባገኘው ፈቃድ፣ በከፍተኛ ጥራትና በልዩ የህትመት ዘዴ በማሳተም፣ ለአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ባለፈው ማክሰኞ በስጦታነት አበርክቷል፡፡ በእለቱ የሩሲያ ፌደሬሽን አምባሳደር፣ የጀርመን ሪፐብሊክ አምባሳደር፣ በኢትዮጵያ የሩሲያ ኩንስትካሜራ ሙዚየም ዳይሬክተር፣ የመንግስት ባለስልጣናት፣ የታሪክ ተመራማሪዎችና የዩኒቨርሲቲ ምሁራን የተገኙ ሲሆን የፎቶግራፍ ኤግዚቢሽንም ተጎብኝቷል፡፡

Saturday, 14 June 2014 12:22

ለማሸነፍ

ጋሻው በጠባቧ ስቱዲዮ ውስጥ በዘረጋት አነስተኛ አልጋ ላይ በጀርባው ተንጋሎ ይቃትታል፡፡ በእልህ ይቃጠላል ፣ በብሽቀት ይወራጫል፣ በምኞት ይንጠራራል . . .
እንደተንጋለለ ዓይኑን ፊት ለፊቱ በሰቀለው ፎቶ ግራፍ ላይ ወረወረ፡፡ እይታው እዚህ ትልቅ ባለቀለም ፎቶ ግራፍ ላይ ካረፈ በቀላሉ አይነሳም፡፡ ቀይ ዳማ ሴት፣  አንገቷን ቀለስ አድርጋ በዓይኖቿ ጠርዝ ታስተውለዋለች፡፡ ዛሬስ «አይ አሸናፊው» እያለች የምታሾፍበት መሰለው፡፡
ትልቁን የሀናን ፎቶ ግራፍ ዘወትር በዓይኑ እንዲዳብሰው ከሚጋብዙት ነገሮች ዋንኛው ዳሌዋ ነው ፡፡
ዳሌዋ ፣ልክ እንደ ዋንጫ ከላይ ሰፋ ብሎ ወደታች እየጠበበ መውረዱ ያስደንቀዋል፡፡
«ወይ የሰው ልጅ !»አለ ባግራሞት «ለካስ የዋንጫን ዲዛይን የኮረጀው ከውብ ሴቶች ዳሌ ነው።
አቤት ተንኮል ! ለካስ ለዋንጫ የመንሰፍሰፋችን ምስጢር ይህ ሆኗል? ሴቶቹም ቢሆኑ ለራሳቸው የአካል ቅርፅ ያላቸው ፍቅር ሳያውቁት ለዋንጫ እንዲሳቡ ያደርጋቸዋል፡፡ እኛም እንዲሁ ሳይገባን የወንድነታችን ስሜት በረቀቀ ሁኔታ ይማልላል. . . » እያለ ይፈላሰፋል፡፡
* * *
. . .  ሃና በፎጣ ተጠቅልላ ከባኞ ቤት እንደወጣች ወደ መኝታ ክፍሏ አመራች፣ ከውስጥ ሆና በሩን ዘጋች፡፡ ያገለደመችውን ፎጣ ከላይዋ ላይ ገፋ በመጠቅለል  ወረወረችው፡፡ ዕርቃኗን ሆነች ፡፡ እየተዟዟረች  ቁመናዋን  ገመገመች  ፣  በተፈጥሮዋ  ተደሰተች፡፡ «የሚሊኒየሙ አሸናፊ ሴት!»  አለችና ፈገግ ፣ ወዲያው ኮስተር፣ እንደመጸየፍ ደግሞ ፈገግ፣ አይኗን ቦዘዝ፣ ሰለምለም . . .   ይህን ጊዜ ጋሻው ወደ አዕምሮው ገባ ፡፡
አፈረች፡፡ እሮጣ  የወረወረችውን ፎጣ አነሳች፣ ተሸፋፍና ቆመች፡፡ ልቧ ደነገጠ፣ ሌሊት በህልሟ አይታዋለች፡፡ ጭልጥ ባለ የሳር ሜዳ ላይ ያገኛታል . . .
በህልሟ፡-
ይቀርባታል «ዛሬ ራቁትሽን ፎቶ ላነሳሽ ፈልጌ ነበር፡፡»
«ምንም ሳልለብስ?»
«አዎ! ዕርቃንሽን ትሆኚና እኔ በማሳይሽ ስታይል
አነሳሻለሁ፡፡ በዚህ ፎቶ የአለም «ሚስ ሞዴሊንግ»  አሸናፊዎች እንሆናለን!»
ትጓጓለች፣  ታቅማማለች፣  ይህን  ጊዜ  ጋሻው  ስውር ይልባታል «እሺ» ትላለች ዛሬ በእውኗ፡፡ ለሕልሙ አለም ጥያቄ በገሃዱ ዓለም መልስ ሰጠች። የሰማት ግን የለም፡፡ ብቻዋን ናት መኝታ ቤቷ ውስጥ፡፡
«እንዴ! ጋሻውንም ልወደው ነው?» ራስዋን በፍርሃት ጠየቀች፡፡ እሷን እንደመውደድ የሚያስፈራት ነገር የለም፡፡
ሰዓቷን ተመለከተች፡፡ ከቶማስ ጋር የመገናኛቸው ሰዓት! «የራሱ ጉዳይ!» አለች ብስጭት ብላ... ሦስት ጊዜ በተከታታይ ቀጥሯት መቅረቷን አልረሳችም፡፡ አሁን ደሞ አራተኛ መሆኑ ነው፡፡
«አሁንስ ያመራል»
«ያምርራ! ምን ያመጣል!» ከራስዋ ጋር ሙግት ገጠመች፡፡ በግቧ መሰረት ማንነቷን ማግኘት፣ የዓለም ምርጥ ሞዴሊስት በመሆን ራሷን፣ ቤተሰቧን፣ ሀገሯን ማኩራት ይጠበቅባታል፡፡ የዚህንም ጊዜያዊ የምስክር ወረቀት ከጋሻው እቅፍ ውስጥ መውሰድ ይኖርባታል፡፡
«የእኔ እጣፈንታ አለማቀፋዊ ዝና ነው! ከጋሻው በቀር የሚቀርቡኝ ወንዶች ሁሉ፣ ሚስት እንድሆናቸው፣ ምግብ እንዳበስልላቸው፣ ልጅ እንድወልድላቸው፣ ምናምን ነው የሚፈልጉኝ። ድንጋዮች! ከእንግዲህ እኔን ለእንዲህ  ዓይነቱ አነስተኛ ዓላማ ማጨቱ አበቃ፡፡
ዛሬ ሄጄ ከምንም በላይ ውድ የሆነ ዓላማዬን መስመር ማስያዝ አለብኝ፣ ሰማይ ጥግ ወደሚገኘው ዙፋኔ አስፈንጥሮ ለሚያደርሰኝ ለጋሻው በመውጣት፣ ፍቅርን በልቡ ማቀጣጠል፣ እሱን የሙጥኝ ይዤ አብሬው መተኮስ. . . »
እቅዷን በሃሳቧ እያውጠነጠነች ከመስታወቱ ዞር ብላ ልብስ መራረጠች፡፡ ከጉልበቷ በላይ የምትንጠለጠል ጉርድ ቀሚስ፣ እንበርቷን የምታሳየው ካኔተራ፣ ክፍት ጫማ፣ ከመስታወቱ ፊት ቆመች ቅልል ያለች ፍልቅልቅ ሴት «እምጵዋ!» የራሷን ምስል ሳመች ፡፡
ብር ብላ ከግቢያቸው ወጣች፡፡ ሚኒባስ ታክሲ መጣ፡፡ የጋቢናውን በር ከፍታ ገባች፡፡ ሹፌሩ ተነቃቃ፣ የሙዚቃውን ድምጽ ጨምሮ ተፈተለከ፡፡
የሞባይል ስልኳ በንዝረት መጥራት ጀመረች፣ ቁጥሩን ተመለከተችው፣ ቶማስ ነው! አላነሳችውም። ደጋግሞ ነዘራት፣ ዝም አለችው «ግፋ ቢል ያቺ ሳንቲሙ ነች የምትቀርብኝ ፣ ዘላለም በሱ ድጎማ እኖራለሁ እንዴ ? ገደል ይግባ !» እያጉረመረመች ወንበሯ ላይ ተመቻቸች፡፡
* * *
ጋሻው ከአስር ለሚበልጡ ዓመታት ፍላጎቱን ገድቦ፣ትዳር ሳይመሰርት፣ ንብረት ሳያካብት ፣ ትኩረቱን በሙሉ ሥራው ላይ በማድረግ ዓለማቀፋዊ አሸናፊነትን ለመቀናጀት ወጣ፣ ወረደ፣ አሸናፊነት እንደከበረ እንቁ ውድ ሆነችበት፡፡ ለበርካታ ጊዜያት፣ ተሳካልኝ ሲል ተንደባሏል፡፡
«አረ የድል ያለህ !» ውስጡ ጮኸ፡፡ እጁን ወደ ራስጌው አካባቢ ሰዶ አንድ ኤንቨሎፕ አወጣ፣ ሲውዲን ፣ እስቶኮልም ሚገኘው ዓለም አቀፍ የፎቶ ግራፍ ውድድር አዘጋጅ ማዕከል የተላከ ነው፡፡ በውስጡ መጽሔት ይዟል፡፡
አሱም የዚህ ውድድር ተካፋይ ነበር፡፡ በመጽሔቱ የላይኛው ሽፋን ላይ አሸናፊ የሆነው የዓመቱ ምርጥ ፎቶ ታትሟል፡፡ ምስሉ አክሊል የደፋች ንግስት በዙፋኗ ላይ እንደተቀመጠች ያሳያል፣ ድባቡ በጣም ደስ አለው፡፡ ፀጥታን ሳይቀር የመዘገበ ድንቅ የእንግሊዝ ሀገር ፎቶ ነው፡፡ ክብር፣ ውበትና ሰላም ይነበብበታል፡፡
መጽሄቱን ገለጠው፣ የሕንድ ቆንጆ! አሁንም
ገለጠው፣ እርጅና በአስፈሪ ክንዱ የደቆሳት የጀርመን አዛውንት! አረጋዊነትን ውብ አድርጎ አቅርቧል፡፡
አሁንም ገለጠው፣ የሩቅ ምስራቅ ልጃገረድ ዓይኗን ጭፍን አድርጋ ተንከተከተችበት! ቶሎ ገለጠው፡፡ አሁንም ገላለጠው! የሱ ሃና የለችም፡፡
እርር አለ! ወደ ፎቶ ግራፍ ሙያ የተሰማራበትን ቀን አስታውሶ ተፀፀተ፡፡ በመስራት ያሳለፋቸውን ከአስር የማያንሱ ዓመታትን ረገመ፡፡ አልቅሶ ቢወጣለት ተመኘ፣ ይህንንም አልቻለም!
በሩ ተንኳኳ. . . ከነ እልሁ፣ ከነብግነቱ ተነስቶ ከፈተው፡፡
ሃና ነች፡፡
ዓይኖቹ የጋለ ብረት መስለዋል፣ በመጀመሪያ ያረፋት በጡቶቿ ክፍላት ላይ ነው፣ ደነገጠ ፡፡
«አንድ» አለች በልቧ፡፡
ከዚያም  እይታው  ቁልቁል  ተንሸራቶ  ጭኖቿ  መሀል ተሰነቀረ፡፡
«ሁለት»
ወዲያው ሽቅብ አነጣጥሮ ከናፍሮቿን ቃኘ
«ሦስት» ፈገግ አለች፡፡
ከመቅጽበት ዓይኖቹን በዓይኖቿ ውስጥ ሰደዳቸው፣ ፍትወተ ሥጋ ቦግ ብሎ ታየው፡፡ አሁን እሱም ሳቀ፡፡ «ታድያስ ሃኒ» እጁን ዘረጋላት፡፡
የቀኝ ጉንጯን አስጠጋችለት፡፡
ሳመው፡፡
የግራ ጉንጯን ሰጠችው፡፡ ደገመው፡፡
ጉንጮቿ የተቀደሱላት መሰላት፡፡ እፎይታ ተሰማት፡፡
ወደ ውስጥ እንድትዘልቅ ጋበዛት፡፡ ሰተት ብላ ገባች . . .
ከሴቶች ጋር የሚኖርህ ቀረቤታ ላይ ጥንቃቄ ማድረግህን አታላላ፡፡ ሴቶቹን ሳይሆን እነሱን ተከትሎ የሚመጣው ትኩረትህን የሚሰርቅህን ስሜት ፍራው፣ ጥላው ሽሸው! ይህ ስሜት ባንተ ላይ ሲበረታ፣ስራ አስፈትቶ በሐሳብ ሲያናውዝ አይተኸዋልና የገዛ ህሊናው አንሾካሾከለት፡፡
ሃና ከስቱዲዮና   መኝታ ቤቱ ጋር በተያያዘችው ጠባብ ሳሎን ውስጥ ነግሳለች፡፡
«ዋው. . . ደረትህ እንዲህ ፀጉር በፀጉር አይመስለኝም
ነበር»
አሁን ይሄ ምን ያስደንቃል? በውስጡ ተቃወመ።
«ወደ ዓርባ ምንጭ እሄዳለሁ ያልከው መቼ ነበር?»
«ነገ ጠዋት አስራ ሁለት ሰዓት ገደማ ከዚህ እወጣለሁ»
ዓይኖቹን ማስቀመጫ እንዳጣለት ዕቃ እያንከራተተ መለሰላት፡፡
«ለምን እኔም አብሬህ አልሄድም? ወደ ደቡብ  እኮ ምንም ሀገር አላውቅም» በዓይኖቿ ቀስፋ ይዛው ትማፀነዋለች፡፡
«በእውነት?»
«ጋሻዬ ሙት ስልህ» ገላዋ ሁሉ በራ፡፡
«እነ ላንጋኖ፣ ሻላ፣ አዋሳ ሐይቆችን አታውቂያቸውማ?»
«የት አባቴ ሄጄ? »
«አዞ፣ ጉማሬ፣ ሰጎን  አይተሸ አታውቂማ?»
«ጋሻዬ ስሞትልህ?» ቅላፄዋ ሊያስፈነጥዘው ደረሰ፡፡ ሁለንተናው ሞቀ «በይ እንግዲህ ለለሊት 12 ሰዓት ተዘጋጂ ፣ እወስድሻለሁ»
«በጣም አመሰግናለሁ ጋሻዬ!»  ተወርውራ ተጠመጠመችበት፤ ዓይኖቹ ከስቱዲዮ ጋር ከተያያዘችው የመኝታ ቤቱ በር ላይ ተጣበቁ፡፡ የተገዛለት አላማ ተፈተነ፡፡
* * *
እሁድ፡፡
ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት፡፡
2000 ዓ.ም
በደቡቡ የኢትዮጵያ ክፍል፣ ከጂንካ ወጣ ብላ የምትገኝ፣ ቃቆ የምትባል ቦታ ላይ ፡-
«ከምድር እኩል የተፈጠረው ንፁህ አየር ይኸውልሽ» አለ ጋሻው እንደ ጥላ የምትከተለው ሃናን እያየ፡፡
«እንዴት ደስ ይላል ! የተራራው አቀማመጥ፣ የዛፎቹ አቋቋም፣ የወንዞቹ አወራረድ» ዙሪያ ገባውን አደነቀች፡፡
«በዚህች ቃቆ በምትባል አካባቢ በና የሚባል የጎሳ መጠሪያ ያላቸው ኢትዮጵያን ይኖራሉ፡፡ ወዲያ ማዶ ደግሞ ማሊ የሚባሉ አሉ ! የሁለቱም ጎሳ አባላት ልብስ የሚባል ነገር አያውቁም፣ እንዲያው ሀፍረታቸውን ለመሸፈን ያህል ብቻ ትንሽዬ ቆዳ ያንጠለጥላሉ. . .»
«አ . .  ሃ . . . ከቡስካ በስተጀርባ የተባለው መጽሀፍ
ውስጥ እንዳሉት ሀመሮች?»
«አዎ፡፡ አንብበሽዋል?»
«እንዴ? ለዛውም ደጋግሜ ነዋ»
«ብራቮ ሃኒ »
ዛሬ በመካከላቸው ከፍተኛ የመሳሳብ ስሜት አለ፣ በየደቂቃው ትደገፈዋለች፣ በየምክንያቱ ያቆላምጣታል፣ ብዙ ያወራሉ፣ በጋራ መምጣታቸውን ወደዱት፡፡
ረጅሙን የዙም ሌንስ በዘመናዊ ካሜራ ላይ እየገጠመ «አሁን እስከ ሁለት ኪሎ ሜትር ርቀት   ማንሳት እችላለሁ!» አላት፡፡
በጣም ተደነቀች፡፡
ካሜራውን ለመግዛት ያየውን ፍዳ እየተረከላት፣ ወንዙ ዳር ያለችው ዛፍ ላይ ወጣና ወዲያ ማዶ ደን ላይ አነጣጠረ፡፡ ምንም የለም፡፡ ወዲህ አነጣጠረ እንደዚያው ነው፡፡ ዱብ ብሎ ወረደ፡፡
በዛፍና ቅጠላ ቅጠሉ መሃል እየተሽሎኮለኩ፣ በሳቅ እየተፍነከነኩ ገላጣ ቦታ ላይ ብቅ አሉ፡፡
አፍረቷ አካባቢ ብቻ ሦስት ማዕዘን ቁርበት ጣል ካደረገች የበና ልጃገረድ ጋር ተፋጠጡ፡፡ ደንግጣ እንደሐውልት ድርቅ አለች የበናዋ ቆንጆ። ጡቶቿ ለመተኮስ የተወደሩ ሮኬቶች ይመስላሉ፡፡ በቀይ አፈር የታሸው ፀጉሯ ቁልቁል ይጥመዘመዛል። ከቀላጭ ብረት የተሰሩ ሦስት ቀለበቶች በአንገቷ ዙሪያ ተጠምጥመዋል፡፡
ሃና አፏን ከፈተች፡፡ የበናዋ ቆንጆ ተክለሰውነት ትንግርት ሆኖባታል፣ ጠይምነቷ ወከክ ያደርጋል፡፡
ጋሻው ቀስ ብሎ ጣቶቹን ከካሜራው ጋር አገናኘ። ልጃገረዲቱ ሃናን በዓይኖቿ ወጋቻት፡፡ ጆሮዎቿም ትልልቅ ሎቲዎችን አንጠልጥለዋል፡፡ ክንዶቿ ከላይ እስከታች በመዳብና ቀላጭ ብረቶች አጊጠዋል፡፡
የጋሻው፣ የሃና፣ የበናዋ ጉብል የልብ ትርታ ቆሟል። የዓይን እርግብግቢት ሳይቀር ተቋርጧል። ፀጥታውን የሚያደፈርስ ጠፋ፣ የበና አሞሮች ክንፋቸውን ሳይቀዝፉ በርቀት ቁልቁል ያስተውላሉ...
የበናዋ ቆንጆ ፊት ላይ ታሪክ ይነበብ ጀመር፡፡ ቁጣ፣ ድፍረት፣ ግርምት!
ጋሻው  ካሜራውን  ዓይኑ  ላይ  ሳያደርግ  በግምት  በማንሳት ተክኗል፡፡ የበናዋ ጉብል አፈገፈገች። የሃና ዓይኖች ልጃገረዲቱ ባዶ እግሮች ላይ አረፉ። አልቦዎቿ አንፀባረቁባት፡፡ ጉብሊቱ አፈገፈገች፡፡ ጋሻው የካሜራውን መምቻ ተጫነ፡፡ ቀጭ!
ቱር አለች እንደሚዳቋ፡፡
«ወይኔ ጋሻዬ አመለጠችህ?» ሃና ጮኸች፡፡
የበና አሞሮች ክንፋቸውን አማቱ፡፡ እነሱም አንቋረሩ ለቆንጇቸው!
ጋሻው ዘሎ ከፍታ ላይ ወጣ፡፡ ካሜራውን ዓይኑ ላይ ነው፡፡ በሌንሱ ውስጥ የጉብሊቱ ምስል ይርመሰመሳል፡፡
«ከሞን!» ይላል ጋሻው ሌንሱን ዞር፣ ቀጭ! ዞር ቀጭ! በተከታታይ የካሜራውን መምቻ ተጫነው፡፡ ፊልሙ ሲያልቅ ቆመ፡፡ በፍጥነት ቀይሮ አነጣጠረ፡፡
የበናዋ ቆንጆ የለችም፡፡
ካሜራውን ለቀቀው፣ አንገቱ ላይ ተንጠለጠለ። ሁለት እጁን ወደ ቃቆ ደመና ወጠረ፣ አምላኩን ማመስገን ሲፈልግ ሁለት እጁን ወደላይ ይወጥራል፡፡
ከከፍታው ላይ ዱብ እንዳለ ካሜራውን ወደ ጀርባው አዞረና ሀናን አቀፋት፡፡
የበና አሞሮች ሌላ ትእይንት ያዩ ጀመር፣ መቅዘፋቸውን ትተው ቁልቁል አሰገጉ. . .
በመጪው ዓመት ካናዳ ቶሮንቶ ውስጥ በሚካሄደው ዓለም አቀፍ የፎቶ ግራፍ ውድድር አሸናፊነቱን ደመነፍሱ ከወዲሁ ሹክ
አለችው፡፡ ስለዚህ ሀናን እንዳቀፋት አንገቷ ሥር ይስማት ጀመር፡፡ የበናዋ ጉብል በስቱዲዮ የታጨቁ ፎቶ ግራፎቹን ነፃ ስታወጣለት ታየው፡፡
ሀና ከናፍርቷን ወደ ከናፍርቱ በመስደድ ላይ ነች፣ ጡቶቿ እስኪፈርጡ ተለጥፋበታለች፡፡
«ሄይ . . . ሄይ . . . ሄይ . . . ጃላ . . .  ጃላ . . .!» ይላል አንድ ሸካራ ድምጽ እንደብራቅ ጮሆ፡፡
ጋሻው ሀናን ለቆ ዞር አለ፡፡
የበናው ወጣት ቁራጭ ቁርበቱን እንዳገለደመ በግራ እጁ ቅቤ የጠጣ በርኮታ፣ በቀኝ ክንዱ የእባብ መርዝ የተለወሰ ቀስቱን እንዳነገበ በኩራት ቆሟል፡፡
ሀና የዓለሟ ፍፃሜ የሆነ መሠላት፡፡
የጋሻው ፊት እንደ በና ፀሐይ አበራ፣ ቅንድቦቹ ሽቅብ ተነሥተው ፀጉሩ ውስጥ ተወሸቁ፡፡ ዓይኖቹ ከመበልጠጣቸው የተነሣ ወልቀው የሚወድቁ እንክብሎች መሰሉ፡፡ ልክ እንደበና አሞሮች ክንፉን ዘረጋ «ሃይ ሃይ ጃል» ብሎ አጸፋውን መለሰ ድምጹ በበና ግዛት ውስጥ አስተጋባ፡
አሞሮቹ ግራ ገባቸው፡፡
ሮጦ አቀፈው የበናውን ወጣት፡፡
እሱም ቀስትና በርኮታውን ቁልቁል ለቀቃቸው፣ ሳሩ ውስጥ ሰጠሙ፡፡
የበናው ወጣት ፈነደቀ ፣ጋሻው ቀልቡን ሳተ «የክፍለ ዘመኑን ፎቶ አገኘህ» እያለች ደመነፍሱ ደስታውን አበዛችለት፡፡
ሀና ራሷን ጠዘጠዛት፣ እያዞራት ነው፡፡
የበናው ወጣት እግሩ ሥር ያስቀመጠውን ቅል ከሳሩ ውስጥ አወጣና ለጋሻው ሰጠው፡፡
ጋሻው አላቅማማም ግጥም አድርጎት ጠጣ፣ ዞሮ ሀናን ያናግራታል «ሀኒ ነይ ወዲህ፣ ይህ ጃላዬ ነው። ተዋወቂው፡፡ በበናዎች ቋንቋ ጃላ ማለት ጓደኛዬ ማለት ነው፡፡ እንዴት ያለ ወዳጄ መሰለሽ . . . » እያለ ቅሉን ይሰጣል «ቅመሺው!»
ጎንጨት ታደርገዋለች፡፡ ቆመጠጣት ቀና ብላ አየችው፡፡
«ዋጭው  ምንም  አይልሽም፣  የማሽላ  ቦርዴ  ነው፣  ጨቃ ይባላል»
ነጭ ነገር ተፋች፡፡
የበናው ወጣት ሳቀ . . .
ጋሻው የበነዋ ጉብል ባሳደረችበት ብሩህ ተስፋ ተነቃቅቷል፡፡ ያለውን ገንዘብ አሟጦ፣ ከሚያውቃቸው ሁሉ ተበድሮ፣ ካነሰውም ንብረቱን በሙሉ ሽጦ፣ ተጨማሪ ፎቶ ግራፎችን ከወሎ፣ ትግራይና ሐረር ማንሣት አለበት፡፡ ከነዚህ መካከል መርጦ በሚልከው በአንዱ ማሸነፉ አይቀርም! ካሸነፈ ሽልማቱ የሃናን ዳሌ የመሰለ ዋንጫ አይደለም፡፡
በአወዳዳሪው  ድርጅት  ስፖንሰር  አድራጊነት  ዓለም  አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ኢግዚቢሽን እንዲያዘጋጅ እድል ይሰጠዋል፡፡ የዕድሜውን አጋማሽ ለሚክል ጊዜ የሰበሰባቸው ፎቶ ግራፎች ቀን  ወጣላቸው  ማለት  ነው፡፡  ተወዳጅ  የሆኑት በጨረታ ይቸበቸባሉ። ያልተሸጡትም ቢያንስ የሀገሪቱን ወርቃማ ባህል፣  ጀግንነት፣ ውበትና ማንነት ለዓለም ሕዝብ በጣፋጭ ለዛቸው ይሰብካሉ።
በኢግዚቢሽኑ የሚያገኘውን ክብር፣ ቱጃር የሚያደርገው ረብጣ ዶላር፣ በቀጣይ ዘመኑ የሚኖረውን የሙያ መሣሪያዎች፣ ያሠራር ደረጃና፣ የአሸናፊነት ሌሎች ፀጋዎች ሁሉ ታዩት፡፡ የጨበጣቸው ያህል እየቋመጠ፣ በቁሙ እያለመ ሳለ ጀምበር በስተ ምሥራቅ እርቃኗን ብቅ አለችለት፡፡ የመጨረሻው ፎቶ ሆና  በካሜራው ጠቀሳት፡፡
ወዲያው   የተከራያት   መኪናን   በመጣችበት   ፍጥነት እያስወነጨፈ ወደ አዲስ አበባ መመለስ ጀመሩ...
ለሊቱን ሙሉ በበናዎች የእሳት ዳር ጨዋታ ሲዝናና ያደረው ጋሻው፣ እጎኑ እንቅልፍ እየጣለ የሚያነሳት ሃናን እረሳ፡፡ ሃሳቡን ከመሪው ጋር እየጠመዘዘ፣ ምኞቱን ከነዳጅ መስጫው ጋር እየተጫነ ያልማል፡፡
እሷ  የሁለት  ዓመት  ምኞትዋ  መና  እንደማይቀር  እርግጠኛ ሆናለች፡፡ አልፎ አልፎ የሽርደዳ ሚመስው ፈገግታዋን ብልጭ አያረገች ትመለከተዋለች፡፡
እሱ እዚህ የለም፡፡ በሃሳብ ጠፍቷል፡፡
ሁለቱን የአሸናፊነት ጥማት ያቃጠላቸውን ተጓዦች የያዘችው መኪና የሶዶ፣ የሻሸመኔ፣ የዝዋይ አየርን ሰንጥቃ ሞጆ ደረሰች፡፡
ተፋላሚዎቹ  የደብረዘይት  ከተማን  ከሩቅ  ሲመለከቱ  ከሃሳብ ጎሬያቸው በመውጣት ተያዩ። አንዳቸው በሌላኛው ዓይን ውስጥ እንግዳ ነገርን አስተዋሉና ተሳሳቁ፡፡
ሁለቱም ድክም ብሏቸዋል፡፡ ማረፍ ይፈልጋሉ፣ ደብረዘይት ምቹ ናት፡፡ ከመኪናው ወርደው ቡና ጠጡ፡፡
«ሳሎኑ ተደፍሯል፡፡ የጉዞ  እቅዶቹ ተካፋይ ሆኛለሁ፣ የስቱዲዮ በር ቀላል ነው ፡፡
የመኝታ ቤቱ ቁልፍ ከተከፈተ አልጋ አለ፣ እዛ ላይ ከወደቅን አለቀ! ይወደኛል፡፡ ይህ ደግሞ ከባድ አይደለም ጊዜ ብቻ ያስፈልገዋል አንጂ. . . » የጣቷን  ጥፍር  በጥርሷ እየከረከመች እራሷን አረጋጋች፡፡
አዲስ አበባ ሲገቡ መሽቷል፡፡ ቤቷ በር ላይ አደረሳት። ጉንጩን ስማው ወረደች፡፡ እንደ እርጥብ ስጋ ቀዘቀዘው፡፡
* * *
ወራት እንዳአቃጠላቸው ፊልሞች ላይመለሱ ጋዩ። በቁርጠኝነት የዘመተበት ውድድር ካሰበው በላይ መስዋት አስከፍሎታል፡፡ የነበረውን ገንዘብ አሟጧል፡፡ ያችኑ ጥቂት ቁሳቁስ ሸጧል፣ የተበደራቸውንም ብሮች በተባለው ጊዜ ባለመመለሱ ቅሬታን አትርፎ መንገድ አጥቷል፡፡
አሁን ጠባቧ ስቱዲዮ ውስጥ፣ ብረት እንደታጠረበት አቦሽማኔ ይንቆራጠጣል፡፡ ከካናዳ ቶሮንቶ የተላከው የተወዳዳሪዎች ውጤት ማስታወቂያ መጽሔት እንደታሸገ ደርሶታል። ኢንቨሎፑን የሚከፍትበት አቅም አጥቶ ይሽከረከራል፡፡
በርግጥ  ኢትዮጵያን  ከዳር  እስከ  ዳር  አካልሎ  ብርቅዬ አእዋፍቷን፣ ድንቅ የመልካ ምድር አቀማመጧን፣ አስገራሚ ቅርሶቿን፣ ታሪካዊ መስህቦቿን ሁሉ ደረጃውን በጠበቀ ብቃት አንስቷል፡፡
አቅሙ የፈቀደውን ሁሉ ቢያደርግም፣ የማሸነፍ ሚስጥሩ የሚፈታው አቅም የፈቀደውን ሁሉ በማድረግ ሳይሆን ጉዳዩ ሊያስከፍል የሚገባውን ዋጋ መክፈል በመቻል ብቻ መሆኑን ማወቁ አስጨንቆታል፡፡
የታሸገው የውጤት ማሳወቂያ ኢንቨሎፕ ውስጥ ያ መፅሔት አለ፡፡ የመፅሄቱ ፊተኛ ሽፋን ላይ ያሸናፊው ፎቶ ይኖራል፡፡ እዚህ አሸናፊ ቦታ ላይ የበናዋ ጉብል ከሌለች ጋሻው ያከትምለታል! በቀጣዩ ጊዜ ስራውን በአግባቡ የሚያከናውንበት የመንቀሳቀሻ አቅም ያጣል፣ ይሰደዳል! አበዳሪዎቹ የቀረውን ካሜራና አንዳንድ ቁሳቁስም ይነጥቁት ይሆናል . . .
በዚህም አለ በዚያ በቀላሉ ለማያንሰራራበት የሞራል ውድቀት፣ የስሜት ስብራት፣ ብሎም መሰረታዊ ፍላጎቶችን ማሟላት የማይችልበት የድህነት ማጥ ውስጥ ይዘፈቃል፡፡
ጭንቀቱን የሚጋራው አጣ፡፡ ላቡ ችፍ አለ በፊቱ ላይ፡፡ በህይወት ዘመኑ የዛሬውን ያህል ጠንካራ ውጥረት ገጥሞት አያውቅም፡፡ አድርጎ የማያውቀወን ቤተአምልኮ ጎራ ማለት አማረው፡፡ እዛ ሄዶ ኢንቨሎፑን ሊከፍት አሰበ፡፡ የበናዋ ጉብል በሚፈልገው ቦታ ከሌለችስ ? እግዚኦ በሉልኝ ! ልል ነው? በራሱ ላይ ዘበተ፡፡
«ቀድሞውንም በዚህች ደሃ ሀገር ውስጥ እየኖርኩ፣ የፎቶ ግራፍ ጥበቡ የመጠቀበት ዓለም ላይ ካሉ ባለሙያዎች ጋር  መወዳደር አልፎ፣ ተርፎም ለማሸነፍ መጎምጀቴ እንዴት
አልፎ፣ ተርፎም ለማሸነፍ መጎምጀቴ እንዴት ያለ ቅዠት ነበር ?» አለ ለራሱ፡፡
ሀይሌ ገብረ ስላሴ በአዕምሮው ተከሰተ፣ የምፀት ፈገግታውን እንደ ካሜራው ፍላሽ ብልጭ አደረገበት፡፡ ዞሮ ፈለገው፣ ድንቅ ፎቶውን በስቱዲዮ ሰቅሏል፡፡ እግሩ  ስር ወድቆ ጭንቀቱን ሊያካፍለው ዳዳውና ፎቶው ፊት ቆመ፡-
«ባላሸንፍስ?»  ጠየቀው፡፡
«ትሸነፋለሃ! »
«መሸነፍ ምንድን ነው?»
«መታገልና ተረትቶ መውደቅ!»
«ማሸነፍስ?»
«ከውድቀት መነሳት!»
«በቃ?»
«አልበቃም»
«ሌላ ማሸነፍ አለ ?»
«አዎ?»
«እባክህ ንገረኝ »
«በውድቀትህ ውስጥ ባለህበት ጊዜ ፣ይህን ውድቀትክን በማሸነፍ እንደምትተካው በፍፁም እምነት ማመን»
«ማመን ብቻ?»
«አሂሂ . . .  ውጤቱ አስኪመጣ ደጋግሞ መሞከር ያስፈልጋል . . .  ይኸውልህ ምን መሠለህ . . . »
እንዳያብድ ሰጋ! ቀልቡን ሰብሰብ  አድርጎ ወደ ኢንቨሎፑ አመራ፡፡
ግድግዳውን ያጣበቡት ፎቶ ግራፎች፣ መደርደሪያው ላይ የተሰቀሉት ካሜራና ሌንሶች ሸምቅቅ እንዳሉ ኢንቨሎፑ ያመጣውን መልዕክት የሚጠባበቁ መስለው።
መንቆራጠጡን ቆም አደረገና አፈፍ አደረገው ኢንቨሎፑን፡፡ ይከብዳል፡፡ በፍጥነት ሊሸረክተው ቆነጠጠ፡፡ አይ! አይ!» ካሜራና ሌንሶቹ ሲንጫጩ ተሰማው፡፡
ፎቶ ሲያድን «ሰላይ!» ተብሎ የታሰረና የተንገላታበት ወቅት፣ በሌሊት ሲማስን በማጅራት መቺ የተዘረፈበትን፣ ጫካ ለጫካ ሲያስስ ከአውሬ መንጋጋ ለጥቂት ያመለጠበትን፣ ገንዘብ እያጠረው የተራበበትን፣ አዕምሮው ጥበቡ ላይ ተጣብቆ ገላው ያደፈበት ልብሱ የመነቸከበትን፣ ጊዜያት አስታወሰ፡፡
የአሸናፊት ጎዳናን የማይሽር የመንፈስ ደዌ  አድርጎ ቆጠረው! ለአመታት የታተረለት አሸናፊነትን ደጋግሞ ረገመው፡፡
የማይቀርለትን ጽዋ ለመጎንጨት ኢንቨሎፑን አነሳ፣ ጠበቅ አድርጎ ከያዘው በኋላ ጥርሱን ነክሶ አይኑን እንደጨፈነ ስቦ አወጣው፡፡ እንደበረደው ህንፃ አገጩ ተርገበገበ፣ ችፍ ያሉት ላቦቹ ተድበልብለው ወደቁ . . .
እንደጨፈነ መጽሔቱን ወደ ኢንቨሎፑ ሊመልሰው አሰበ፡፡ አላደረገውም! ዓይኑን ገለጠው። ከበናዋ ጉብል ጋር ተፋጠጡ! ፊቷ ላይ ታሪክ ይነበባል፡፡ ቁጣ፣ ድፍረት፣ ግርምት! ጋሻው አፈገፈገ የስቱዲዮ ግድግዳ አገደው፡፡ ህልም እንዳይሆን ሰጋ፡፡
መጽሔቱን ወደ ዓይኑ አስጠጋ፣ ሮኬቶቿ አነጣጡሩበት፣ በቀይ አፈር የታሸው ጥምዝ ፀጉሯ፣ የአንገት ቀለበቷ፣ ሁሉም
አሉ፡፡  በእጁ  ዳበሳት  አልደነበረችም፡፡  እቅፍ  አደረጋት፡፡  ሰላም ሰጠችው፡፡
«አላልኩህም»  እያለች ጮኸች ደመነፍሱ «በል ሳማት»
አዘዘችው፡፡
መጽሔቱን ሳመው፡፡ የስቱዲዮ በር ተበረገደ፡፡ አቅሉን ስቶ ወጣ፣ አስፋልት አቋረጠ፣ ታክሲ ያዘ፣ ርቆ ወረደ በተለያዩ ቅያሶች እያሰባበረ ገስግሶ እነ ሃና ሳሎን፣ በሃና ፊት ተገኘ፡፡
ሃና ጆሮ የሚበጥስ ጩኸት አሰማች፡፡ እናቷ ተንደርድረው ገቡ፡፡
መጽሔቱን እያሳየች የሆነው ሁሉ አነበነበችላቸው፡፡
ከቁብ ሳይቆጥሯት ገርምመዋት ወጡ፡፡
መጽሔቱን ገለጠችው፡፡ የግሪክ እመቤት!
ጋሻው ከጥይት ያመለጠ መሰለው፡፡
አሁንም ገለጠችው፣ የአርመን ኮረዳ ፡፡
ሃና ደነዘዘች፡፡ ገለጠችው የሩስኪ ውብ፡፡ ገለጠችው የህንድ…
የበናዋ ጉብል ናፈቀችው፡፡ መጽሔቱን ከሃና ቀማትና ወደ ሽፋኑ መለሰው፣ ሮኬቶቿን ወደረችበት። መጽሔቱን ሳመው፣ ፆታዊ ፍቅር ተፀነሰበት፡፡
«አገባታለሁ! » ሲል ተናገረ፡፡
«ምን»
«ሚስቴ አደርጋታለሁ!»
«ም . . .  ምን አልክ ጋሻዬ? » “እቺ ናት ሚሰቴ፣ አ ገ ባ ታ ለ ሁ”
«እውነት የምትለውን ታደርገዋለህ? አንተእኮ… እኔ…» የምትናገረው ጠፋት፡፡ «ይሆናል የኔ ጌታ? በመካከላችሁ ያለውን ሰፊ የባሕል ፣ የአኗኗር፣ የስልጣኔ፣ ልዩነት አላስተዋልከውም? ይህን ያህል የተራራቀ ልዩነት ያላቸው ሰዎች በትዳር ሊጣመሩ ይችላሉ? ጋሻዬ? ይቻላል ጋሻዬ?. . . »
ሀይሌ ገብረስላሴ ፈገግ አለ፡፡ ያ ህያው ምስል በጋሻው ሕሊና ደግሞ ተከሰተ፡፡ ጋሻውም እሩቅ እያለመ፣ እሩቅ እያሰበ አብሮት ፈገግ አለ፡፡
ሃና ይህን የመሰለው በረከት ተቋዳሽ ባለመሆኗ ከልቡ አዘነላት፡፡ በጓደኝነት ስሜት ጠልቆ መረመራት፣ ጉድለቷን አስተዋለ፡፡ ከሕይወት ፍልስፍናው ይበልጥ ሊያካፍላት፣ እምነቱን ሊተክልባት ወሰነ። «ይሄውልሽ ሃንዬ. . . ጉዳዮችኮ ቀላል ወይም ከባድ ስለሆኑ አይደለም የሚሳኩልን፣ ልናሳካቸው በቆራጥነት ስንወስንና ያላማቋረጥ ስንጥር ብቻ ነው የሚሳካልን፡፡» የግል እምነቱን አሰረፀባት፡፡
ምንም እንኳን ጋሻውንና ያልጨበጠችውን ዓለማቀፋዊ ዝናን፣ ተስፋ አድርጋ የቶማስን ንፁህ ወዳጅነት ብትረግጥም፣ መልሳ ልታገኘውና እስከ መጨረሻውም በፍቅሩ ውስጥ ልትሆን እንደምትችል አመነች፡፡ ልታደርገውም ወሰነች፡፡
ወዲያው በአይነ ህሊናዋ እንዲህ ይታያት ጀመር።
የበና ማኅበረሰብ ገላቸው በልብስ ተሸፍኖ። በምሽት፣ መስክ ላይ በሚያነዱት እሳት ዙሪያ ተሰባስበው፣ በርኮታቸው ላይ ቁጢጥ እንዳሉ፣ አረቄያቸውን እየተጎነጩ ሲጨዋወቱ . . .
ጨረቃ ፍልቅልቅ ብላ ቁልቁል ስታስተውላቸው...
እሷ እና ቶማስ ጎን ለጎን እንደተቀመጡ፣ እሳቱን እየሞቁ በሹክሹክታ ሲያወጉ. . .
የበናዋ ጉብል   ጠይሙ ፊቷን በፈገግታ አስጊጣ፣ በዘመናዊ የቆዳ ጃኬት የተሸፈኑ ውድር ሮኬቶችዋን በማስቀደም  ወደ ጋሻው
ስትርብ . . .
ጋሻውም በርኮታው ላይ ጉብ እንዳለ ፣በነበልባሉ ውስጥ አሻግሮ እየተመለከታት በነደደ ስሜት ሲጠብቃት. . .
ጨረቃም እየተቅለሰለች ደመናው እቅፍ ውስጥ ስትሸሸግ . . .

Published in ልብ-ወለድ
Saturday, 14 June 2014 12:20

የጸሐፍት ጥግ

ጭንቅላቴን ባዶ ለማድረግ መፃፍ አለብኝ፡፡ ያለዚያ አቅሌን እስታለሁ፡፡
ሎርድ ባይረን
በመፃፍ ካልተነፈስክ፣ በመፃፍ ካልጮህክ ወይም ካልዘመርክ አትፃፍ፡፡ ምክንያቱም ባህላችን ለፅሁፍ ቦታ የለውም፡፡  
አናይስ ኒን
ከሌላ ፀሃፊ ባለሁለት ቃላት ሃረግ ከምሰርቅ ሙሉ ባንክ ዘርፌ ብያዝ እመርጣለሁ፡፡
ጃክ ስሚዝ
ፅሁፍ ከዝምታ ጋር የሚደረግ ትግል ነው፡፡
ካርሎስ ፉንቴስ
ህትመት የሰውን አዕምሮ ለጨረታ ማውጣት ነው፡፡
ኤሚሊ ዲኪንሰን
የደራሲ ሁለቱ እጅግ ማራኪ ጥንካሬዎች፣ አዳዲስ ነገሮችን የተለመዱ ማድረግና የተለመዱትን አዲስ ማድረግ ናቸው፡፡
ሳሙኤል ጆንሰን
ለመፃፍ የተገደድክበትን ምክንያት እወቀው፡፡ ስሩን በልብህ ውስጥ ማሰራጨቱንም አረጋግጥ። መፃፍ ብትከለከል ብቸኛ አማራጭህ ሞት እንደሆነ ለራስህ ተናዘዝ፡፡
ሬይነር ማርያ
ጥሩ ልቦለድ የዋና ገፀ ባህሪውን እውነት ሲነግረን፣ ቀሽም ልቦለድ የደራሲውን እውነት ይነግረናል፡፡
ጂ.ኬ.ቼስቴርቶን
በአንድ ሰው አዕምሮ ውስጥ በሺዎች የሚቆጠሩ ሃሳቦች ይኖሩታል፡፡ ያ ሰው ብዕሩን አንስቶ እስኪፅፋቸው ድረስ ግን እኒያ ሃሳቦች መኖራቸውን አያውቅም፡፡
ዊሊያም ሜክፒስ ታክሬይ
በእያንዳንዱ ጭንቅላት ውስጥ ያለውን የትራፊክ መጨናነቅ የሚያስወግዱ መፃህፍት መፃፍ እፈልጋለሁ፡፡
ጆን አፕዳይክ
ሰዎች በደምስሮቼ ውስጥ ቀለም፣ በትየባ ማሽኔ ቁልፎች ላይም ደም ማግኘታቸው አይቀርም፡፡
ቴሪ ጉይሌሜትስ
መፃህፍቱ ራሳቸው እንዲወለዱ ፈለጉ እንጂ እኔ አልፈጠርኳቸውም፡፡ ወደ እኔ መጥተው “እንዲህና እንዲያ ሆነን ካልተፃፍን” ብለው ወትውተውኝ ነው፡፡
ሳሙኤል በትለር

Published in ጥበብ
Page 10 of 18