Saturday, 21 June 2014 14:39

ያልተጋበዙ እንግዶች

            እነዚህ እንግዶች አውቀንና ፈቅደን፣ ቄጠማ ጎዝጉዘንና ፈንዲሻ ቆልተን፣ ቡና አፍልተን፣ ምግብ አዘጋጅተን፣ … “ቤት ለእንቦሳ” ሲሉን “እንቦሳ እሰሩ” በማለት በደስታና በፌሽታ የምንቀበላቸው አይደሉም፡፡ ካለእኛ ፈቃድና እውቅና ውስጣችን ገብተው በመኖር ምግባችንን የሚጋሩንና (በአብዛኛው ሕፃናትን ለሞት) የሚዳርጉ አደገኛና አስጠሊታ ተውሳኮች ናቸው፡፡
እንግዲህ እኛ የሰው ዘሮች በዚህች ምድር ከማንኛውም በላይ እጅግ የተሳካልን እንስሳም አይደለን?! ስለዚህ በርካታ አደገኛና አጥቂ (ትላትሎች) ከእኛ ጋር በጥገኝነት ለመኖር ይወሩናል። በዚህ የተነሳ በብዙ መቶ የሚቆጠሩ ቫይረሶች፣ ባክቴሪያዎች፣ ፈንገሶች፣ ፕሪቶዟና አርትሮፓድስ የመሳሰሉ በርካታ ባለአንድ ህዋስ ጥገኛ ፍጡሮች (ሴል) መኖሪያ ነን፡፡
እነዚህ በዓይን የማይታዩ ባለ አንድ ሴል ደቂቅ ነገሮች ከተፈጠሩ በኋላ በመጀመሪያ ቫይረሶች ባክቴሪያን ይመርዛሉ ወይም ኢንፌክት ያደርጋሉ፡፡ በዚህ ሂደት ባለ አንዱ ሴል ወደ ባለ ብዙ ሴሎች (መልቲሴሉላር) ፍጡር ከተለወጡ በኋላ፣ በእነሱ እግር የበለጠ ውስብስብ የሆኑ ፍጡሮች ይተካሉ። በምድር ላይ ከሚገኙ 100 ሚሊዮን ወይም ከዚያ በላይ ከሚሆኑ ፍጡራን መካከል ግማሽ ያህሉ ጥገኛ ህዋሳት ሳይሆኑ አይቀሩም፡፡
ዲክሰን ደስፖሚየ፤ በዓይን የሚታዩ ጥቃትን ህዋሳት (ትላትሎች) ተመራማሪ (ሜይክሮባዩስት ዮሎጂስት) ናቸው፡፡ ተመራማሪው እነዚህን ያልተጋበዙ እንግዶች ለይተን አውቀን በውስጣችን መኖሪያቸውን እንዳይሰሩ ጥንቃቄ እንድንናደርግ፣ በሚያደርሱት የጉዳት መጠን ከ1ኛ እስከ 10ኛ ደረጃ ያሉትን ጎጂ ጥገኛ ትሎች ለይተው አቅርበዋል፡፡ ጉዳቱ አነስ ከሚለው እንጀምር፡፡
10ኛ. ቦት ፍላይት (Botfly-Dermatobia hominis)፡- እነዚህ ጥገኛ ትሎች ከባድና ትላልቅ ሲሆኑ መገኛቸውም የመካከለኛ አሜሪካ የባህር ዳርቻ መዝናኛዎች ናቸው፡፡ ሰዎች እነዚህን ትላልቅ ጥገኛ ትሎች ሰውነታቸው ላይ ሲያዩ ወዲያው እንቁላሎቻቸውን ሳይጥሉባቸው ጠርገው ስለሚያስወግዷቸው እቅዳቸው አይሰምርም፡፡ እነሱ ምናቸው ሞኝ ነው? የመጀመሪያው ዘዴ ካልሰራ፣ ሌላ ረቀቅ ያለ ዘዴ ይቀይሳሉ፡፡ ሁለተኛው ዘዴ ዕንቁላል መጣያቸውን በቀላሉ የማይታወቅ (የማይጠረጠር) ማድረግ ነው፡፡ ለዚህ ተልዕኮ የተመረጠችው ደግሞ ሴቷ የወባ ትንኝ ናት፡፡ ዕንቁላሉ ሳይፈለፈል ዕጫቸውን ሴቷ የወባ ትንኝ ሆድ ላይ ይጥላሉ፡፡
ዕጩን የተሸከመችው የወባ ትንኝ ሰው ነድፋ ደም ስትመጥ፣ ዕጩ፣ ከተጠቂው ሰውነት በሚያገኘው ሙቀት ይፈለፈልና ተጠቂው ሰውነት (ቆዳ) ላይ ይወድቃል፡፡ ከዚያም ቆዳውን ሰርስሮ ወደ ውስጥ በመግባት፣ ከቆዳ ስር ባሉት ሕዋሳት (ሴሎች) ውስጥ ሆኖ ለእድገት የሚያስፈልገውን ምግብ እያገኘ፣ ከ5 ሳ.ሜ በላይ ርዝመት እስከሚኖረው ድረስ ለበርካታ ሳምንታት እዚያው ይቆያል፡፡ ጥገኛ ትሎቹ የሚፈልጉትን ዕድገት ካገኙ በኋላ፣ በገቡበት አኳኋን ከቆዳ ውስጥ ወጥተው መሬት ላይ ይወድቁና ዕጭ ይፈጥራሉ፡፡ ከቀናት ቆይታ በኋላ ከዕጩ ውስጥ ቦትፍላይ ትሎች በመውጣት፣ አዲስ የሕይወት ዑደት (ላይፍ ሳይክል) ይጀምራሉ፡፡
9ኛ. ወስፋት (Ascaris Lumbricoides)፡- ይህን የእርሳስ መጠን ያለውንና መኖርያው ትንሹ አንጀት ውስጥ የሆነውን ሞላላ ጥገኛ ትል ብዙዎቻችን እናውቀዋለን፡፡ ይህ ጥገኛ ትል በሆድ ውስጥ ሆኖ ምግብ ስልቀጣን ወይም መፈጨትን በማስተጓጎል፣ ምግብ ለማግኘት አንቲትራፕሲን የተባለ ኬሚካል ያመነጫል፡፡ በዚህ አይነት የምግብ መተላለፊያ በመዝጋት ምግብ ያገኛል፡፡
ሴቶቹ የወስፋት ትሎች ከሶስት እስከ አምስት ዓመት ዕድሜ ሲኖራቸው፣ በየቀኑ 200ሺ ዕንቁላሎች ይጥላሉ፡፡ እነዚህ ዕንቁላሎች ከሰገራ ጋር ወጥተው አፈር ላይ ያድጋሉ፡፡ ዕንቁላሎቹ እድል አግኝተው እስኪፈለፈሉ ድረስ ለዓመታት እዚያው ይቆያሉ፡፡
ይህ ሞላላ ጥገኛ ትል በመላው ዓለም በዓመት ሁለት ቢሊዮን ሰዎችን የሚያጠቃ ሲሆን ከዚህ ውስጥ አብዛኞቹ ህፃናት ናቸው፡፡ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባቸው ትናንሽ ህፃናት ይቀጭጫሉ፤ የማሰብ፣ የማመዛዘንና የመረዳት ችሎታቸው ይቀንሳል፡፡
ወስፋት በሰውነት ውስጥ ከቦታ ቦታ የሚንቀሳቀሰው ከመጠን ያለፈ ትኩሳት፣ ለምሳሌ ከፍተኛ የወባ ትኩሳት ሲኖር ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ከተለመደው ከሰገራና ከአፍ ውጪ በሌላ መንገድ ሊሰደዱ ይችላሉ፡፡ በዚህ ሁኔታ ጉበት፣ ጣፊያ ወይም የሐሞት ከረጢት ከተወረሩ፣ የወስፋት ጉዳት ወይም ኢንፌክሽን በጣም አጣዳፊና አደገኛ ሊሆን ይችላል፡፡ ከዚህ በስተቀር የወስፋት ህክምና ቀላል ነው፤ መበንዳዞል የተባለው መድኃኒት ከተወሰደ ድራሻቸው ይጠፋል፡፡
8ኛ. ዊፕ ዎርም (richuris trichiura) ይኼኛው ጥገኛ ተውሳክ ሞላላ ነው፡፡ መኖሪያው ትልቁ አንጀት ውስጥ ሲሆን፣ መገኛው ደግሞ ምድር ወገብ አካባቢ ነው፡፡ አንድ ህፃን አፈር ላይ የወደቀ ነገር አንስቶ ወደ አፉ እስኪከት ድረስ እንደ ሌሎች ሞላላ ትሎች ሁሉ፣ የዚህም ትል ዕንቁላል፣  ያለአንዳች እንቅስቃሴ አፈር ላይ ይቆያል፡፡
ይህ ጥናት ትል አብዛኛውን ጊዜ በህፃናት ላይ የሚያስከትለው ተቅማጥ ነው፡፡ ነገር ግን ብዙ ማማጥ ፊንጢጣ ወደ ውጭ እንዲወጣ ያደርጋል፡፡ ወደ ውስጥ ለመመለስ ደግሞ የፊንጢጣ ጡንቻዎች ስለሚላሉ ጥረቱን ከባድ ያደርገዋል፡፡ ወደ ውጭ የወጣውና የረጠበው የፊንጢጣ ዙሪያ ባደጉ የጥገኛ ትሎች መወረር ደግሞ በጣም አስጠሊታና አዕምሮን የሚረብሽ ሁኔታን ይፈጥራል፡፡ ሆኖም ግን በሽታው በጊዜ ከታወቀ ሕክምናው ቀላል ነው፡፡ ይህ አስቀያሚ ትል 50 ሚ.ሜ ሊረዝም ይችላል፡፡
7ኛ. የቻጋስ በሽታ (Trypanosoma Cruzi)፡- ይህ ባለ አንድ ሴል አጥቂ መገኛው ደቡብና መካከለኛው አሜሪካ ሲሆን መተላለፊያው ደግሞ ደም የምትመጥ “Kissing bug” የተባለች በራሪ ነፍሳት ናት፡፡
የዚህች ነፍሳት መጥፎ ባህርይ በምትመገብበት ጊዜ (ደም ስትመጥ) ሰውን መመረዟ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ደግሞ ጥገኛ  ትሉ ወደ ተጠቂው የደም መዘዋወሪያ ገብቶ ቻጋሲ ዲዝስ ለመፍጠር በጣም የሚፈልገው አጋጣሚ ነው፡፡
ይህ ጎጂ አውሬ ወደ ሰውነት ክፍል ይጓዝና በአቅራቢያው ያገኛቸውን ሴሎች በመውረርና በተጠቃው አካባቢ የፍቅር ምልክት (Roman’s sign) የተባለ እብጠት እንዲፈጠር ያደርጋል፡፡
የዚህ አውሬ ጥቃት በጣም አደገኛ የሚሆነው፣ ወደ ልብና የነርቭ ሲስተም ወይም ወደ ትንሹና ትልቁ አንጀት ከሄደ ነው፡፡ በነርቭ ሴሎች ላይ የሚያደርሰው ጉዳት የሰውነት ብልቶቻችን (ልብ፣ ሳንባ፣ ኩላሊት፣…) ተግባራቸውን እንዲያቋርጡና ከነበራቸው መጠን በላይ እንዲያድጉ ያደርጋል፡፡ የዚህ አውሬ ጥቃት ብዙ ጊዜ ከቆየ የፊንጢጣ (ሜጋ ኮብሎን) የምግብ መተላለፊያ (ሜጋ ኤሶፋጋስ) እንዲጎዳና ልብ ከመጠን በላይ እንዲያድግ ያደርጋል፡፡
6ኛ. ጊኒ ዎርም (Darcunculus medinesis):- እነዚህ ሞላላ ጥገኛ ትሎች፣ ዕንቁላላቸውን ለማስተላለፍ የሚጠቀሙት ብዙ ጊዜ የረጋ ኩሬ ውሃ አካባቢ የሚገኙትን የውሃ ትንኞች ነው፡፡ እነሱን በመንደፍ ዕጮቻቸውን ወደ ትንኞቹ ያስተላልፋሉ፡፡ ትንኞቹ ደግሞ የጊኒ ዎርም ዕጮች እንደያዙ ውሃው ላይ ይሞታሉ፡፡
አንድ ሰው የጊኒ ዎርም ያለበት የረጋ ውሃ ከጠጣ፣ ሰውነት፣ ዕጮቹን የያዘውን ትንኝ ሲፈጭ ወይም ዳይጀስት ሲያደርግ ትሎቹ ነፃ ይወጣሉ፡፡ ነፃ የወጡት ሴትና ወንድ ትሎች ከጥቂት ወራት በኋላ ግንኙነት ይፈጥራሉ፡፡ ወንዶቹ ግንኙነቱን ካደረጉ በኋላ ከሰውነት ጋር ይዋሃዳሉ፡፡ ሴቶቹ ግን ወደ እግርና ወደ እግር መዳፍ ይጓዛሉ፡፡ እዚያ ከደረሱ በኋላ ዕንቁላላቸውን የሚጥሉበትን ስፍራ ያሳብጣሉ፡፡ እብጠቱ የሚያቃጥል ኃይለኛ ሕመም ስለሚፈጥርበት፣ ሰውዬው ፈውስ ፍለጋ ወደ ውሃ ስፍራ ይሄዳል፡፡ በዚህ ጊዜ እብጠቱ ይፈነዳና ዑደቱ እንደገና ይጀመራል፡፡
ብዙ ጊዜ ህክምናው የትሉን ጭንቅላት ቀጭን ነገር ላይ ጠቅልሎ ትሉ ተነቅሎ እስኪወጣ ድረስ ቀጭኑን ነገር ማዞር ነው፡፡ እስካሁን የተመዘገበው የጊኒ ትል ርዝመት 78 ሴ.ሜ ነው፡፡
5ኛ. ዝሆኔ ወይም ሞላላ ትል (wicheria bancrofti)፡- የዚህ ሞላላ ትል መኖርያ፣ ሰውነታችን ተጠቅሞ የሚያስወጣውን ተረፈ ምርት ለማስወገድ በሚጠቀምበት ነጭ የደም ሴል በሆነው ንፁህ የሰውነት ፈሳሽ (ሊፍም-Lymph) ውስጥ ነው፡፡ እነዚህ ትሎች ካደጉ በኋላ ለዓይን የማይታዩ ጥቃቅን (Microfilariae) ህዋሳት እየፈለፈሉ ለ10 ዓመታት ይኖራሉ፡፡ ጥቂት ህዋሳት ደግሞ ደም ውስጥ ይገቡና የወባ ትንኝ ሰው ሲነድፍ፣ ከደም ውስጥ ወደ ትንኟ ይገቡና ወደ በሽታ ፈጣሪ ዕጭነት ይቀየራሉ፡፡
የተመረዙ ዕጮችን የተሸከመችው የወባ ትንኝ በሌላ ጊዜ እንደገና ሰው ስትነድፍ፣ ዕጮቹ፣ የወባዋ ሰለባ ወደሆነው ሰው ይተላለፋሉ፡፡ ከዚያም ተነድፎ ወደቆሰለው ቦታ ይዋኙና መኖርያቸው ወደሆነው ነጭ የደም ሴልና ንፁህ ሰውነት ፈሳሽ መያዣ ይገቡና እስከ እርጅናቸው እዚያው ይኖራሉ፡፡
ያረጀው ሞላላ ትል ሲሞት፣ የፈሳሹ መተላለፊያ ቀልቶ ያብጥና የፈሳሹን ፍሰት ይቀንሳል፡፡ ሁሉም ያረጁት ትሎች ሲሞቱ፣ የፈሳሽ መተላለፊያው ሙሉ በሙሉ ይዘጋል፡፡ ከዚያም እብጠቱ ይቀጥልና እግሮች ትልቅ ይሆናሉ፣ የሰውነት ቆዳ ደረቅ ይሆንና ይተጣጠፋል፡፡
4ኛ. ኤስፖንዲያ (Leighmania braziliensis)፡- ይህ ባለ አንድ ሴል ጥገኛ ትል ወደ ሰውነት የሚገባው የአሸዋ ዝንቦች (sand fly) በነከሱት ቀዳዳ ነው፡፡ ጥገኛ ትሎቹ ሰውነትን ከመረዙ በኋላ፣ በሰውነት ውስጥ በመዘዋወር የበሽታ መከላከያ አቅም የሚፈጥሩትን ህዋሶች (ሴሎች) ወርረው ይመርዛሉ፡፡ እነዚህ የተመረዙ ሴሎች ወደ አፍ፣ ፊንጢጣና ወደ ሽንት ቧንቧ ይጓዛሉ፡፡ ጥገኛ ትሎቹ እዚያ አምሳያቸውን አዲስ ትሎች ፈጥረው፣ ህዋሳቱ ተመርዘው እንዲያመረቅዙ (አልሰር) እንዲሆኑ ያደርጋሉ፡፡ ይህ ጥገኛ ትል ካልታከመ በስተቀር አደገኛና አጣዳፊ ችግር ሊፈጥር ይችላል፡፡
በዚህ ጥገኛ ትል የተመረዘ አፍ ካልታከመ በስተቀር በከፍተኛ ደረጃ ያመረቅዝና የላይኛው የአፍ ሪያ ሊናድ ይችላል፡፡ ይህ ሁኔታ ‹ኤስፓንዲያ› የሚባል ሲሆን የሚገኘውም የሕክምና ሰዎች አዘውትረው በማይገኙበት ጭልጥ ያለ ገጠር ነው፡፡ አንዴ ህክምና ካገኘ የሚድን ሲሆን የአፍ መተላለፊያውን በቀዶ ህክምና ወደ ቀድሞው ደረጃ መመለስ ይቻላል፡፡
3ኛ. የአሳማ ኮስ ትል (Taenia Solium)፡- በትንሷ አንጀት የሚኖረው የአሳማ ኮሶ ትል 4 ሜትር ሊረዝም ቢችልም በአንፃራዊነት ሲታይ አይጎዳም ማለት ይቻላል፡፡ ሰዎች በዚህ ትል የሚያዙት ትሉ ያለበትን ጥሬ ወይም በደንብ ያልበሰለ የአሳማ ስጋ በመብላት ነው፡፡
ወጣት የሆነው የዚህ ኮሶ ትል በህብረ ህዋስ ውስጥ ካለው ቅርፊት ይወጣና በሶስት ወር ሙሉ ትል እስከሚሆን በሚቆይበት ትንሹ አንጀት ግድግዳ ላይ ይጣበቃል፡፡ ዕንቁላሎቹ ናቸው ትንሽ የበለጠ አደገኛ የሆኑት፡፡ ዕንቁላሎቹ ከተበሉ በጣም ጥቃቅን ዕጮች ከደም ጋር እየተዘዋወሩ፣ መኖሪያቸውን የልብ፣ የአንጎልና የዓይን ህብረ ህዋሳት በማድረግ እስከ ወጣትነት ያደርጋሉ፡፡ ከእነዚህ አደገኛ ጥገኛ ትሎች መገላገል የምንችለው መድኃኒት ወስደን ከሰገራ ጋር በማስወጣት ብቻ ነው፡፡
2ኛ. የውሻ ኮሶ ትል (Echinococcus granulosus)፡- ይህ ውሾችን የሚያጠቃ ትንሽ ትል ሲሆን ወደ ሰውም ሊተላለፍ ይችላል፡፡ አብዛኛውን ጊዜ የዚህ ትል አስተላላፊ በጎች ናቸው፡፡ ይህ ትል ያለበት በግ ሲታረድ፣ ወጣቶቹን ትሎች የያዘውን ጉበቱን ውሾች ይበሉታል፡፡        
አንዴ ውሾቹ ከበሉትና ትሉ መኖሪያ ካገኘ በኋላ፣ ወጣቶቹ ትሎች ከቅርፊታቸው ውስጥ ይወጡና በውሻው አንጀት ላይ ተጣብቀው እስከ አዋቂነት ያድጋሉ፡፡ በኮሶ ትሉ የተጠቁት ውሾች በሺዎች የሚቆጠሩ አዋቂ የኮሶ ትሎች ማኖር ይችላሉ፡፡ አዋቂዎቹ ትሎች እንቁላል ሲጥሉ እንቁላሎቹ ከውሻው ሰገራ ጋር ይወጣሉ፡፡ በጎች ደግሞ እንቁላል ያለበትን ቅርፊት በመብላት ትሉን ወደ ውስጣቸው ያስገባሉ፡፡
የበግ አርቢዎችም ከቅርፊቱ ጋር ንኪኪ ሲያደርጉ በኮሶ ትሉ ሊያዙ ይችላሉ፡፡ ቅርፊቱ ከተሰነጠቀ ኢንፌክሽኑ አንጎልና ሳንባ ወደ መሳሰሉ ሌሎች ብልቶች በመሰራጨት ሞት ሊያስከትል ይቻላል፡፡
1ኛ. የዓይን ትል (Loa Loa)፡- አብዛኛውን ጊዜ ሞላላ ትሎች የሚኖሩት ከቆዳ ስር ሲሆን በሰውነት ውስጥ ሲዘዋወሩ የሚያደርሱት ጉዳት ቀላል ነው፡፡ ሴቶች ትሎች የሚጥሏቸው ዕጮች ከደም ጋር ይቀላቀሉና በአጋዘን ዝንቦች ይበላሉ፡፡ ዕጮቹ መርዛማ እስኪሆኑ ወደ አፍ አካባቢ ጡንቻ ከመሸጋገራቸው በፊት በዝንቦች የክንፍ ጡንቻዎች ላይ ያድጋሉ፡፡ በትሉ የተጠቃው የአጋዘን ዝንብ፣ ሰውን ሲነክስ ዕጮቹ እየዳኹ ወደ ቆዳና ዝንቡ ወደነከሰው ቁስል ይሄዳሉ፡፡ በበሽታው የተጠቃ ሰው በመስታወት ዓይኑን ሲያይ፣ ትሉን ዓይኑ ውስጥ  ሊያይ ይችላል፡፡ ትሎች ዓይን ውስጥ ከገቡ በቀዶ ህክምና መውጣት አለባቸው፡፡   

Published in ዋናው ጤና

ሲመረጡ “ልከኛ” የነበሩ የፓርላማ አባላት “ዙጦ” ሆነዋል

      የደቡብ አፍሪካ መንግስት ለበርካታ ዓመታት ኤችአይቪ/ኤድስን ለመቆጣጠር ከፍተኛ ትግል ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ የጤና ባለሙያዎች እንደሚሉት፤ አሁን ትኩረቱን ከልክ በላይ ውፍረት ላይ ማድረግ አለበት፡፡ መቀመጫውን ለንደን ባደረገው “Lancet” የተሰኘ የህክምና ጆርናል ላይ የታተመ ዓለም አቀፍ ጥናት እንዳመለከተው፤ ከደቡብ አፍሪካ አዋቂ ሴቶች ውስጥ 70 በመቶ ያህሉና 40 በመቶው ወንዶች ከልክ በላይ ወፍራሞች ናቸው፡፡ ልጆቹም ቢሆኑ ከውፍረት አላመለጡም ይለናል ጥናቱ፡፡ ሩብ ያህሉ ልጃገረዶችና 20 በመቶ የሚሆኑ ወንድ ልጆች ሲበዛ ወፍራም ናቸው፡፡ በዚህም የተነሳ ከስኳር በሽታ እስከ ልብ ህመም ድረስ ላሉ ደዌዎች የመጠቃት ዕድላቸው ከፍተኛ ነው - ዘ ኢኮኖሚስት እንደዘገበው፡፡
በደቡብ አፍሪካ ብቻ ሳይሆን በቀሩት የአፍሪካና ሌሎች ድሃ አገራትም በቀጣዮቹ ሁለት አስርት ዓመታት ከልክ በላይ የሆነ ውፍረት በከፍተኛ መጠን እንደሚጨምር የጠቆመው ጥናቱ፤ ከመጠን ያለፈ ውፍረት ከከተሞች መስፋፋትና ከኢኮኖሚ ዕድገት ጋር ተያይዞ የሚከሰት እንደሆነ አመልክቷል። ህፃናት በምግብ እጥረት በከፍተኛ ደረጃ በሚቀጭባቸው አካባቢዎች የአዋቂዎች ከልክ በላይ ውፍረት ይበልጥ እየጨመረ መምጣቱ አያዎ (Paradox) ነው ብለዋል-ተመራማሪዎች፡፡
ከልክ በላይ ውፍረት ለተለያዩ በሽታዎች የሚያጋልጥ ቢሆንም አብዛኞቹ ደቡብ አፍሪካውያን ግን በውፍረታቸው ደስተኞች ናቸው፡፡ የኑሮ ዘይቤያቸውንና የአመጋገብ ልማዳቸውንም የመቀየር ፍላጎት የላቸውም፡፡ ቃለ-መጠይቅ ከተደረገላቸው 25ሺ500 ደቡብ አፍሪካውያን መካከል 88 በመቶ የሚሆኑት አሪፍ ነው ብለው የሚያምኑት የሰውነት አቋም ወፍራምነትን እንደሆነ ጥናቱ ይጠቁማል፡፡
የጤና ሚኒስትሩ አሮን ሞትሶአሌዲ ግን በዚህ አይስማሙም፡፡ የህክምና ዶክተር የሆኑት ሚኒስትሩ፤ ጠዋት የእግር ጉዞ በማድረግና ጤናማ የአመጋገብ ልማድን በመተግበር  መሸንቀጥ እንደሚገባ አርአያ በመሆን እያሳዩ ይገኛሉ፡፡ የሥራ ባልደረቦቻቸው የእሳቸውን ምሳሌነት እንዲከተሉ ያደረጉት ጥረት ግን አልተሳካም፡፡
በያዝነው ወር መጀመርያ ላይ የደቡብ አፍሪካ የፓርላማ አባላት ካፊቴሪያቸው  ከልክ በላይ ለሆነ ውፍረት የሚዳርጉ ምግቦችን ያቀርባል ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡ አባላት ሲመረጡ “ጥሩና ልከኛ” ነበሩ ያለችው የአፍሪካ ብሄራዊ ኮንግረስ የፓርላማ አባል ሼይላ ሲትሆል፤ “አሁን ግን ሁሉም ዙጦ ሆነዋል” ብላለች - ዘ ኢኮኖሚስት እንደዘገበው።
በነገራችሁ ላይ ኢትዮጵያን በተመለከተ የወጣ ጥናት እንደሚጠቁመው፤ ለጊዜውም ቢሆን ከልክ በላይ ውፍረት እኛን አያሰጋንም፡፡ ሌላ የሚያሰጋን ነገር ግን አልጠፋም፡፡ ውፍረቱ ኢትዮጵያ ውስጥ የሌለው አመጋገባችን ላይ የተለየ ጥንቃቄ አድርገን አይደለም፡፡ በከተማ መስፋፋትና በኢኮኖሚ ዕድገት ገና በመሆናችን ነው፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ የእንግሊዙ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ባወጣው ሪፖርት፤ ኢትዮጵያ በድህነት ከዓለም በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ይፋ አድርጓል - ከኒጀር ቀጥሎ ማለት ነው፡፡ ጐበዝ ድህነትን ለማጥፋት ብዙ ትጋትና ረዥም ጉዞ ይጠብቀናል፡፡ ግን የማይቻል ነገር የለም!!       


Published in ዋናው ጤና

የምግብ ጭማሪ ምንድነው?
የምግብ ጭማሪ ማለት እንደ ምግብ አካል የሚቆጠር ሲሆን ምግብን ለማጣፈጥ፣ ለማቅለም፣ ሳይበላሽ ለማቆየት ወይም ለማሳመር የሚረዳ በምግብ ላይ የሚጨመር ማንኛውም ንጥረ ነገር ነው፡፡
የምግብ ጭማሪዎች በምግብ ውስጥ ለምን ይጨመራሉ?
የምግብ ጭማሪዎች የተለያዩ ጥቅሞች ያሉት ሲሆን ከዚህ በታች የተዘረዘሩት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
የምግብን ደህንነትን ለመጠበቅ - የተለያዩ የምግብ ጭማሪዎች ምግብን ለብክለት የሚያጋልጡ እንደ ሻጋታ፣ የተለያዩ ፈንገሶችና ባክቴሪያዎች እንዳይራቡና እንዳያድጉ ምቹ ያልሆነ ሁኔታን በመፍጠር ምግቡ ለረጅም ጊዜ ሳይበላሽ አገልግሎት ላይ እንዲውል ለማድረግ ጥቅም ላይ ይውላሉ፡፡
ተፈጥሯዊ የምግብ ንጥረ ነገርን ማሻሻል - የተለያዩ የምግብ ንጥረ ነገሮች እንደ ቫይታሚን፣ መዓድናት፣ ፋይበሮችና ሌሎች ለሰውነታችን አስፈላጊ የሆኑ ንጥረ ምግቦችን በተለያዩ የምግብ ጭማሪዎች መልክ በማዘጋጀት፣ በተፈጥሮ ምግቡ ውስጥ ያልነበረውን ወይም በተፈጥሮ ምግቡ ውስጥ የሚገኝ ቢሆንም በተለያዩ የምግብ ዝግጅቶች ወቅት የሚወገዱትን የምግብ ንጥረ ነገሮችን በመተካት፣ የምግቡን የንጥረ ነገር ይዘት በማሻሻል፣ በነዚህ ንጥረ ምግቦች እጥረት ሊከሰቱ የሚችሉ የህብረተሰብ የጤና ችግሮችን ለመከላከል ይረዳል፡፡
የምግብ ቃናን፤ ጣዕምን፣ ልስላሴንና እይታን ያሻሽላሉ - የተለያዩ ምግብ ጭማሪዎች በምግብ ውስጥ የሚጨመሩት የምግቡን ጣዕም ለመጨመር፣ ቃናውን ለማሻሻል፣ ቀለሙን ከተፈጥሯዊ ቀለሙ በማሻሻል ሳቢ ወደ ሆነ ቀለም ለመለወጥ እንዲሁም ልስላሴን በመጨመር የምግቡን ተፈጥሯዊ ይዘት በማሻሻል የምግቡን ተፈላጊ ለማድረግ ነው፡፡
የምግብ ጭማሪ ጥራትና ደህንነት ቁጥጥር
የምግብ ጭማሪን ምግብ ውስጥ በመጨመር የምግብን ተፈጥሯዊ ባህሪ በመለወጥ፣ የምግቡን ተወዳጅነት ለማሳደግ የሚደረገው ተግባር ከአባቶቻችን ጋር የቆየ ባህል ነው፡፡ ለምሳሌ ጨውን ፈጭቶ እንደ ሥጋና ዓሣ በመሳሰሉት በከፍተኛ ሁኔታ የሚበላሹ የምግብ አይነቶች ውስጥ በመጨመር፣ የምግቦቹን የመጠቀሚያ ጊዜ ለማስረዘም ይጠቀሙበት ነበር፡፡ የተለያዩ ቅመማ ቅመሞችን በመጠቀምም የምግቦቹን ጣዕምና ቃና የተሻለ ያደርጉ  ነበር፡፡
በአሁኑ ጊዜም ህብረተሰቡ ጣዕሙና ቃናው የተሻለ፣ በተለያዩ የምግብ ንጥረ ነገሮች የበለፀገ፣ ደህንቱ ተጠብቆ ለረዥም ጊዜ ሊጠቀምበት የሚችልና እይታው ማራኪ የሆነ ምግብ ለማግኘት ፍላጐቱ ከፍተኛ በመሆኑ፣ የተለያዩ የምግብ አምራች ድርጅቶች የተለያዩ የምግብ ጭማሪዎችን መጠቀም፣ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መጥቷል፡፡
የምግብ ጭማሪ ጥራትና ደህንነት አስመልክቶ፣ ከፍተኛ ሳይንሳዊ ምርምሮች እየተደረጉም ይገኛሉ፣ በሀገራችንም የነዚህን የምግብ ጭማሪዎች ጥራታቸውንና ደህንነታቸውን ጠብቀው ለህብረተሰቡ እንዲደርሱ የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድኃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደር እና ቁጥጥር ባለስልጣን፣ የተለያዩ የጥራትና ደህንነት ማረጋገጫ ሥራዎችን እያከናወነ ነው፡፡ ከነዚህም መካከል በሀገር ውስጥ እንዲሁም ውጭ አገር ተመርተው ወደ ሀገራችን በመግባት ለህብረተሰቡ እየቀረቡ የሚገኙትን የምግብ ጭማሪዎች ጥራትና ደህንነት ለማረጋገጥ የተለያዩ የቁጥጥር ስራዎችን ያከናውናል፡፡
ህብረተሰቡም የቁጥጥሩ ባለቤት በመሆን፣ የራሱን ጤና ራሱ ይጠብቅ ዘንድ፣ የምግብ ጭማሪዎች ጥራታቸውንና ደህንነታቸውን የጠበቁ እንዲሆኑ ለማረጋገጥ የሚከተሉትን ነጥቦች ማጤን ይጠበቅበታል፡፡
የምግቡን ጭማሪ ይዘትና ባህሪ በተቻለ መጠን ማወቅ፣
ሊያስከትል የሚችለውን የአጭርና የረዥም ጊዜ የጤና ችግር መገንዘብ፣
የምግብ ጭማሪው ማሸጊያ ላይ የተለጠፈውን ገላጭ ጽሑፍ በትኩረት መመልከትና ቢያንስ የሚከተሉትን መረጃዎች ያካተተ መሆኑን ማረጋገጥ:-
የምግብ ጭማሪው የንግድ ስም፣
የምግብ ጭማሪው አምራች ድርጅት፣ ስምና ሙሉ አድራሻ፣
የምግብ ጭማሪው በሌላ ምግብ ላይ በሚጨመርበት ጊዜ በምን ያህል መጠን መሆን እንዳለበትና ምን አይነት የባህሪ ለውጥ በምግቡ ላይ እንደሚያመጣ የሚገልፅ ጽሑፍ መኖሩን ማየት፣
በማሸጊያው ላይ በግልፅ “የምግብ ጭማሪ” የሚል ጽሑፍ መፈለግ፣
ምግቡ የተመረተበትና የመጠቀሚያ ጊዜው የሚያበቃበት ቀን፣
የምርት መለያ ቁጥር፣
የምግብ ጭማሪው አግባባዊ የአጠቃቀም፣ የአያያዝና የጥንቃቄ ሁኔታ የሚጠቁም ጽሑፍ መታተሙን ምግቡን ከመግዛቱና ከመጠቀሙ በፊት በጥሞና ተመልክቶ ማረጋገጥ ይኖርበታል፡፡
ምንጭ፡ (“የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና ጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን” የተገኘ)   

Published in ዋናው ጤና

             በአርባ ምንጭ የአዞ እርባታ ጣቢያ ለጉብኝት ታድመናል፡፡ የጣቢያው አስጎብኚ ወ/ት ህይወት አሰፋ ትባላለች፡፡ ስለ አዞ አፈጣጠር ስታብራራ መስማት ያልፈለገን ሰው ሳይቀር በማራኪ አቀራረቧ እንዲያደምጣት ታስገድዳለች፡፡ አቀራረቧ እስከዛሬ በርካቶቻችን ስለ አዞ የምናውቀውን እውነታ አጥርቶ ትክክለኛ መረጃ እንድንይዝ የሚያደርግ ነው፡፡ ህይወት የተረከችውን የአዞ አፈጣጠር እንዲህ አቅርቤዋለሁ፡፡
“የአዞ ተፈጥሮ በህይወት አንደበት”
ሃይቅ ዳርቻ ላይ አዞ እናት ከውሃው ከ20 እስከ 30 ሜትር ትርቅና፣ 60 ሣ. ሜትር ያህል አሸዋውን ቆፍራ እንቁላሎቹን ትቀብራለች፡፡ እንቁላሎቹ አዞ ለመፈልፈል 90 ቀናት ይበቃቸዋል፡፡ ጫጩት አዞ ገና እንደተፈለፈለ አሸዋ ውስጥ ሆኖ ድምፅ ማሰማት ይችላል፡፡ አንድ አዞ ከ 3 ዓመት እስከ 6 ዓመት ባለው ጊዜ ውስጥ ለእርድ ይደርሳል፡፡ አዞ አናቱ ካልተመታ አይሞትም፡፡
የሚታረደውም እንደሌሎች የእርድ እንስሳት ከአንገቱ ስር ሳይሆን በጀርባው በኩል ነው፡፡ ምክንያቱም የስረኛው ቆዳ እጅግ ተፈላጊ ስለሆነ እንዳይጎዳ ነው፡፡
ቆዳቸው እስከ 400 ዶላር ይሸጣል፤ ስጋቸው ግን በማርቢያ ጣቢያው መልሶ ለራሳቸው ምግብነት እየዋለ ቢሆንም እየተገነባ ያለው ዘመናዊ ቄራ ሲጠናቀቅ፣ ሃገሪቱ የአዞ ስጋ ወደ ውጭ ትልካለች፡፡ አንድ ኪሎ የአዞ ስጋ በአሁኑ ወቅት እስከ 160 ዶላር ይሸጣል።
የአዞን ፆታ ለመለየት በሚገባ ስለ አዞ የሚያውቁ ሰዎች ያስፈልጋሉ፡፡ ማንም ሰው በእይታ ብቻ ይሄ ወንድ ነው፣ ይህቺ ሴት ነች ብሎ መለየት አይችልም። ባይን የሚታይ የፆታ መለያ አዞ ጨርሶ የለውም፡፡ የአዞዎች የፆታ ሁኔታ በባለሙያዎች የሚለየው የተፈለፈሉበትን አሸዋ ሙቀት በመለካት ነው፡፡ ሙቀቱ ከፍተኛ ከሆነ ወንዶች ይሆናሉ፤ ቀዝቀዝ ካለ ሴቶች ይሆናሉ፡፡
እናት አዞ፤ በአሸዋ ውስጥ የቀበረችውን እንቁላል በየጊዜው እየተመላለሰች ደህንነቱን ትከታተላለች። ከተፈለፈሉ በኋላ ድምፃቸውን ከአሸዋ ውስጥ ስትሰማ በአፏ እየያዘች ታወጣና ውሃ ዳር ሳር ውስጥ ታስቀምጣቸዋለች፡፡ ይህን የምታደርግበት ምክንያት ጫጩት አዞዎች ትናንሽ ነፍሳትን እንዲመገቡ ነው፡፡ በሌላ በኩል በውሃ ውስጥ የሚገኙ ትላልቅ አዞዎች እንዳይበሉባትም ለመከላከል ነው፡፡ እናት አዞ ልጆቿን ከአደጋ ለመጠበቅ ዛፍ ላይ ወጥታ 360 ዲግሪ እየተመለከተች በትጋት ቅኝት ታደርጋለች፡፡
ጫጩት አዞዎች ከጥርስ ጋር ስለሚፈጠሩ ገና ከአሸዋ ውስጥ ሲወጡ መናከስ ይጀምራሉ። የጥርሳቸው ብዛት ከ62 እስከ 66 ይደርሳል፡፡ አዞ በነዚህ ጥርሶቹ እየቆረጠ ዋጥ ማድረግ እንጂ ማኘክ፣ ማላመጥ የሚባል ጣጣ አያውቅም። ከስጋ ውጪም አዞ ሌላ ምግብ አያውቅም። አዞ ተንቀሳቃሽ ምላስ የለውም፤ ለዚህ ነው የማያላምጠው፡፡
አስጎብኚያችን ህይወት እዚህ ጋ ጥያቄ ልጠይቃችሁ አለች፡፡ የአዞ እንባ የሚባለው ምንድን ነው? አዞ ምግብ ሲበላ ያለቅሳል የሚባለውስ? ብላ ጠየቀችን፡፡ በርካቶች የመሰላቸውን ሞከሩ፤ አንዳቸውም ግን መልሱን አላወቁትም፡፡ እኔው መልስ ልስጥ አለችን፡፡
አዞ ቆዳው ጥቅጥቅ ነው፡፡ የላብ ማስወጫ የለውም። በብዛት ቆርጦ ሲውጥ ጉሮሮው ይጨናነቃል፡፡ ጎሮሮው ሲጨናነቅ ላብ ያልበዋል፡፡ ላቡ በአይኑ በኩል ይወጣል፡፡ ስለዚህ የአዞ እንባ ላብ ነው፡፡ አዞ ያስለቅሳል እንጂ አያለቅስም” አለችን፡፡
ስለ አዞ አንዳንድ እውነታዎች
አንዲት አዞ በአንድ ጊዜ ከ30-70 የሚደርስ እንቁላል ትጥላለች፣ በአመት አንድ ጊዜ ብቻ የምትጥል ሲሆን 85 በመቶው ይፈለፈላል። በአለም ላይ 25 ዓይነት የአዞ ዝርያዎች ሲኖሩ አራቱ በአፍሪካ ይገኛሉ፡፡ሰ በኢትዮጵያ የሚገኘው አደገኛው የናይል አዞ የሚባለው ብቻ ነው፡፡
አንድ ትልቅ አዞ ከ7-8 ሜትር ሲረዝም፣ ከ500-700 ኪ.ግ ይመዝናል፡፡ ከ120-150 አመትም ይኖራል፡፡ የአዞ ቆዳ በአለማቀፍ ደረጃ እጅግ ተፈላጊ ሲሆን ከ27-37 ሣ. ሜትር ስፋት ያለውና ሽንቁር የሌለው ንፁህ ቆዳ 1ኛ ደረጃ ተብሎ እስከ 400 ዶላር ይሸጣል፡፡





Published in ህብረተሰብ

ውሸት ራሱን የቻለ በሽታ ሳይሆን የበሽታ ምልክት ነው
ሃሰተኛ የትምህርት ማስረጃ - መዋሸት ሳይሆን ማጭበርበር ነው
ውሸት ወደ ስብዕና ደረጃ ከተሸጋገረ፣ ግለሰቦቹ ችግር እንዳለባቸው አይቀበሉትም

ውሸት ምንድን ነው?
ውሸት ራሱን የቻለ የስብዕና መለያ ሊሆን ይችላል፡፡ የተለያየ እድሜ ላይ ሊከሰትም ይችላል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ከጨቅላነት እድሜ የሚጀምር ሲሆን አንዳንድ ጊዜ ደግሞ በጉርምስና ጊዜ ይጀምራል፡፡ ውሸትን ከልጅነት እድሜ ጀምሮ እየተሸለመ የመጣ (ሲዋሽ በቤተሰቡ ትኩረት እየተሰጠው ያደገ) ህፃን እድሜ ልኩን ውሸትን በልማድና በስብዕና መለያነት ይዞት ይኖራል፡፡
ሌላው የውሸት አይነት በስብዕና ቀውስ መዛባት የሚመጣ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ውሸት ለማህበረሰብ ጠንቅ የሆነ የስብዕና አይነትን ይፈጥራል፡፡ ሰዎችን ማታለል፣ ወዳልሆነ አቅጣጫ መምራት የመሳሰለው ተግባር እንደ አንድ መጥፎ የስብዕና መለያ ምልክት ይወስዳል፡፡ ስለሆነም እነዚህ የስብዕና መዛባት ችግር ያለባቸው ሰዎች ውሸት አንደኛው መለያቸው ይሆናል፡፡
በሌላ በኩል የአዕምሮ ጭንቀት ህመም ለውሸት መነሻ ምክንያት ይሆናል፡፡ የጭንቀት ህመም በጉዳት ወቅትና ከጉዳት በኋላ የሚፈጠር ሲሆን ይህ ጭንቀት ሰዎችን ከእውነተኛው ስብዕናቸው እንዲያፈነግጡ ያደርጋቸዋል፡፡ ሰዎች በአንድ ምክንያት ከተጎዱ በኋላ ሚደርስባቸው የጭንቀት ህመም፣ ያንን ጉዳታቸውን እያስታወሱ ላለመሰቃየት ሲሉ ሌላ ያልሆነ ነገር በመፍጠር መዋሸት ይቀጥላሉ፡፡ እንዲህ አይነቱ ሰዎች ሆን ብለው በመዋሸት ሌላውን ለመጉዳት የሚታትሩ አይደሉም፡፡ ያንን ጉዳታቸውን ላለማስታወስና ወደ ጉዳታቸው ላለመመለስ የሚዋሹ ናቸው፡፡
ውሸት በሽታ ነው?
ውሸት ራሱን የቻለ በሽታ ሳይሆን የበሽታ ምልክት ነው፡፡ ከላይ ለመግለፅ እንደተሞከረው ውሸት የስብዕና መዛባት ችግር፣ የጭንቀትና ከፍተኛ የአእምሮ ጉዳት ምልክት ነው፡፡ ለምሳሌ የስብዕና መዛባት ችግር ያለበት ሰው ውሸት አንዱ ምልክቱ እንጂ ከዚያ በላይ በርካታ መለያዎች ይኖራሉ፡፡ በሌላ በኩል “Boarder light” የሚባል የስብዕና ችግር አለ፡፡ ሲሆን ይህ ችግር ስሜታቸው የሚቀያየርና ከሰዎች ጋር ያላቸው መስተጋብርና ከማህበረሰቡ ጋር ያላቸው ግንኙነት የሚለዋወጥ ግለሰቦች ላይ የሚታይ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ስሜታቸውን መቆጣጠር የማይችሉ፣ ግልፍተኝነት የሚያጠቃቸውና፣ በማህበራዊ ግንኙነታቸው ችግር ያለባቸው ሰዎች የሚያንፀባርቁት የስብዕና አይነት ነው - “ቦርደር ላይ የሚባለው፡፡ እነዚህ ሰዎች ስሜታቸው ለመቆጣጠር ጥረት የሚያደርጉ ሲሆን በዚህ በሚያደርጉት ጥረት ውስጥ ስለሚዋሹ አንዱ የስብዕናቸው መለያ ይሆናል እንጂ ውሸት ራሱን የቻለ በሽታ አይደለም፡፡
ውሸትን ማንኛውም ሰው ይዋሻል፡፡ የማይዋሽ ማንም የለም፡፡ በየትኛውም የእውቀትና እድሜ ደረጃ እንዲሁም አኗኗርና ባህል ውስጥ ያለ ሰው ይዋሻል፡፡ ማንኛውም ሰው ትክክለኛነትን ማረጋገጥ ስለማይችል ህይወቱን ለማስተካከል፣ ስጋቶቹን ለመቅረፍ የሚዋሽበት ሁኔታ ይፈጠራል። ሰዎች ውሸትን እንዲዋሹ ከሚያተጓቸው ነገሮች አንዱና ዋናው የፍርሀት ስሜት ነው፡፡ ፍርሀት የሚከሰትባቸው በርከት ያሉ መሰረታዊ ምክንያቶች ያሉ ሲሆን አንደኛው ትችትን ነቀፌታን ውርደትንና ሸንፈን ያለመቀበል ነው፡፡ ሌላኛው ምክንያት ደግሞ አንድ ግለሰብ በአንድ በቡድን ወይም ማህበረሰብ ውስጥ ራሱን የቻለ ማንነት ይኖረዋል፡፡ ይህን ማንነቱን የሚያጎድልበት ነገር ካለ ያንን ለመሙላት ሲል ሊዋሽ ይችላል፡፡
በሌላ በኩል ህልውናን ለማስጠበቅ፣ በስነ ልቦና ችግርና የተፈላጊነትን ስሜት ለመጨመር የሚዋሽበት ጊዜ አለ፡፡ ለምሳሌ እድሜን ቀንሶ መናገርን ማንሳት ይቻላል፡፡ እድሜያችን እየጨመረ ሲሄድ ተፈላጊነት እያጣን እንደምንመጣ ስለምናስብ ፍርሃት ይለቅብናል፡፡ ከዚህ ከፍርሀት ለመላቀቅ እንዋሻለን። በእነዚህና መሰል ምክንያቶች የማይዋሽ ሰው አለ ማለት ይቸግራል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ውሸት “reaction formation” ይባላል፡፡ ይህ ምን ማለት ነው… እራሳችንን ከእውነተኛው ነገር በተቃራኒው የማሰብ ሂደት ላይ ማድረግ ማለት ነው፡፡ ባሉብን ጉድለቶች የተነሳ አዕምሯችን ጭንቀት ላይ እንዳይወድቅ የማድረግ ሂደት ነው… ሪአክሽን ፎርሜሽን፡፡ ለምሳሌ አንዲት ሴት አንድን ወንድ አፍቅራው በሰው ፊት እንዳላፈቀረችው ትናገራለች፡፡ ይህ ምንድነው? ውሸት ነው፡፡ የምትዋሸው ደግሞ በምትኖርበት ማህበረሰብ ውስጥ ያላትን ዋጋ ላለማጣት ስትል ነው፡፡ የበታችነት ስሜት እንዳይሰማት ያደረገችው ትግል ነው፡፡ ማለት ይቻላል፡፡ ይህቺ ሴት በዋሸችው ውሸት ታማሚ ናት ወይም ትክክል አይደለችም ብሎ ለመደምደም ይቸግራል፡፡ ይህቺ ሴት ሌላውን ለመጉዳት፣ በሌላው ላይ ችግር ለመፍጠር አልተጋችም፡፡
ስንት አይነት ውሸታም አለ?
ውሸታሞች በሁለት ይከፈላሉ፡፡ የመጀመሪያዎቹ በማንኛውም ቦታ፣ ጊዜና ሁኔታ የሚዋሹ ሲሆን ሁለተኛዎቹ በተወሰነ ጊዜና ቦታ ብቻ የሚዋሹ ናቸው፡፡ እነዚህ ውሸቶች ቀደም ብሎ እንደተጠቀሰው የተለያዩ ናቸው፡፡
ሰሞኑን በትምህርት ማስረጃ ውሸት የፈፀሙት ግለሰብ የውሸት አይነት የትኛው ነው?
ሰሞኑን በተለያዩ ሚዲያዎች መነጋገሪያ የሆነው የአቶ ሳሙኤል ዘ/ሚካኤል ጉዳይ በቴክኒክ ደረጃ ስንመለከተው ውሸት አይደለም፡፡ እንደሚባለው ፈፅመውት ከሆነ አይን ያወጣ ማጭበርበር ነው። ውሸት ማለት ትርጉሙን ስንመለከት በዕለት ተዕለት የህይወት መስተጋብር ውስጥ ያልተገባ መረጃን መልቀቅ ማለት ነው፡፡ የእለት ተዕለት ማህበራዊ መስተጋብር የሚከወነው በጓደኛሞች፣ በስራ ባልደረቦች፣ በቤተሰብ አባላት፣ በጎረቤታሞች መካከል ነው፡፡ በነዚህ መካከል የሚካሄድ ትክክል ያልሆነ የመረጃ ዝውውር ነው ውሸት የሚባለው፡፡
ከላይ የተጠቀሱት ግለሰብ ድርጊት ግን ከውሸት አልፎ “ማጭበርበር” የሚለውን ደረጃ የሚዝ ነው፡፡ ማጭበርበር ደግሞ “ናርሲስት” የሚባለው የስብዕና አይነት ውስጥ ሊመደብ ይችላል፡፡ አለበለዚያም ለማህበረሰብ ጠንቅ የሆነ የስብዕና ምድብ ውስጥ ሊካተት ይችላል፡፡
ሆኖም ይሄ ከውሸት አልፎ ከፍተኛ የሆነ ራሱን የቻለ ምድብ ውስጥ ሊመደብ የሚችል ነው፡፡ የግለሰቡ ግን ከውሸት አልፎ ከፍተኛ የሆነ የማጭበርበርና የማታለል ተግባር ውስጥ የሚካተት ነው፡፡ ይህ የማጭበርበር አይነት ለማህበረሰብ ጠንቅ የሆነ የስብዕና ባለቤቶች የሚያንፀባርቁት ነው ሌሎችን በማታለልና በመጉዳት ለራስ ጥቅም ብቻ መሮጥ ከውሸት በላይ ነው፡፡ ውሸት በማህበራዊ መስተጋብር ስሜታዊ በሆኑ ጉዳዮች ውስጥ የሚደረግ ስሜትን ያዘለና በአንደበት የሚነገር ነው፡፡ ማጭበርበር ግን ፍፁም ከውሸት ይለያል፡፡ የዓለም አይኖች ሁሉ እኔ ላይ ይረፉ፤ በዚህም ገንዘብ ላግኝ በማለት፤ በተቋማት፣ በአገርና በትልልቅ ግለሰቦች ስም መነገድ ማጭበርበር እንጂ መዋሸረት አይደለም።
ለምሳሌ አንዲትን ሴት ፍቅረኛው ለማድረግ የሚዋሽ ወንድ አሊያም ውርደትንና ሽንፈትን ላለመቀበል ጓደኛውን ወይም ፍቅረኛውን የሚዋሽ ግለሰብ፣ ህዝብን በጅምላ ከሚያጭበረብር ግለሰብ ጋር እኩል አይደለም፡፡ አገርን፣ መንግስትን፣ ህዝብን፣ በድፍረትና በማናለብኝነት የሚያጭበረብር ሰው ከፍተኛ የሆነ የግብረገብነት ችግር የተጠናወተው ነው፡፡ ከፍተኛ የሆነ የግብረገብነት ችግር ያለበት ሰው ደግሞ መቼም ቢሆን ከማጭበርበር የሚያግደው ስሜት አይኖረውም፡፡ የሞራል ልዕልናም የለውም። ስለዚህ የጤናማ መንፈስና አስተሳሰብ ድሀ ነው ማለት ይቻላል፡፡ እንደዚህ አይነት ሰው የኋላ ታሪኩ የጤንነቱ ሁኔታና ያለፈበት የህይወት መንገድ መጠናት አለበት፡፡   
ከፍተኛ የግብረ ገብነት ችግር ከጉርምስና ጊዜ ጀምሮ (ከ18-21 ዓመት ባለው) የሚከሰት ሲሆን ለማህበረሰብ ጠንቅ የሆነ ስብዕናን ያዳብራል፡፡ ለምሳሌ አደንዛዥ ዕፅ መጠቀም፣ ጠብ አጫሪነት፣ ድብድብ፣ ስርቆት፣ ማታለልና ማጭበርበር የግብረገብነት ችግሮች ሲሆኑ ለህብረተሰብ ጠንቅ የሆነ የስብዕና መዳረሻዎች ናቸው፡፡
የበላይነት ስሜት (ናርሲስት ፐርሰናሊቲ) የሚባለውም ከሰው በላይ ሆኖ ለመታየት ከሁሉም እበልጣለሁ ማለት፣ የሁሉንም ትኩረት ጨምድዶ ለመያዝ የሚደረግ የአምባገነንነት ስሜት የተጠናወታቸው ነገር ግን ከመጀመሪያውም የግብረ ገብነት ችግር አብሯቸው ያደገ ሰዎች የሚያሳዩት ነው፡፡ እነዚህ ግለሰቦች ይህን ፍላጎታቸውን ለማሳካት ብዙ ርቀት ይጓዛሉ፡፡ ከውሸትም በጣም ይዘላሉ፡፡ ለምሳሌ የሰሞኑ አጀንዳ የሆኑት ግለሰብ፤ ሀሰተኛ የትምህርት ማስረጃ አላቸው ከተባለ፣ ያጭበረበሩት ጓደኛቸውን፣ ጎረቤታቸውን ወይም የስራ ባልደረባቸውን አይደለም፡፡ ህዝብን፣ መንግስትን፣ አገርን ነው፤ ይህ ደግሞ ወንጀል ነው። ለምሳሌ ምንም ሳይኖራቸው በአንድ ዩኒቨርሲቲ ማህተም የተዘጋጀን ማስረጃ ማቅረብ ውሸት ተብሎ የሚታለፍ አይደለም፤ ማታለል ነው፡፡
መፍትሄው ምንድን ነው?
ችግሩ ሳይከሰትም ከተከሰተም በኋላ መፍትሄ አለው፡፡ በነገራችን ላይ ውሸት ወደ ስብዕና ደረጃ ከተሸጋገረ፣ ግለሰቦቹ ራሳቸው ችግር አለብን ብለው አይቀበሉም፡፡ ነገር ግን የመንግስትና የማህበረሰብ ተቋማት ይህንን ችግር የሚፈቱበት የራሳቸውን አሰራር በመዘርጋት መፍታት ይችላሉ፡፡ ተቋማቱ የውሸቱን አይነት ጥልቀትና የሚያደርሰውን ጉዳት በመመልከት በውሸቱ መጠን የተቃኘ መፍቻ ስልት ይነድፋሉ ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ቤተሰብ ራሱን የቻለ ተቋም እንደመሆኑ ልጆችን በማሳደግ ሂደት ውስጥ የራሱን ሚና ሊጫወት ይገባል፡፡ ይህ ማለት ልጆች በግብረ ገብ እንዲያድጉ፣ ሌላውን እንዲወዱ፣ ከሌላው ሰው ጋር ተግባብተውና ተስማምተው መኖርን እንዲለማመዱ፣ ለሌላው ሰው ትክክለኛ ነገርን በመስጠት ትክክለኛ ነገርን መሸለም እንዲችሉ አድርጎ ማሳደግ በወላጆች ላይ የሚጣል ኃላፊነት ነው፡፡
አንዴ በውሸት ተግባር ላይ ተሰማርተው የሚገኙትን ደግሞ በዚህ ችግር ውስጥ መኖራቸው ለእነሱም ሆነ ለሌላው ሰው ጎጂ መሆኑ ሊነገራቸው ይገባል፡፡ በትክክለኛ መንገድ ትክክለኛ ነገር ማግኘት እንደሚችሉ እንዲሁም ለራሳቸው ያላቸውን ግምት እንዲያስተካክሉ ተናግሯቸው በመረጃ ደረጃ ካወቁት በኋላ፣ የስነ-ልቦናና ሌሎች መሰል ድጋፎችን በማድረግ መፍትሄ መስጠት ይቻላል፡፡  

Published in ባህል
Saturday, 21 June 2014 14:29

ብርቅዬው ብሔረሰብ

61 ብቻ ሲቀሩ፤ 12ቱ ብቻ ቋንቋውን ይናገራሉ
እባብ ለቁጥራቸው መቀነስ አስተዋፅኦ አድርጓል

      የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች ህዝቦች ክልል የ56 ብሔሮች መገኛ ነው፡፡ ከነዚህ መካከል 16 ያህሉ ዋና መናገሻቸውን ጂንካ ከተማን አድርገው በደቡብ ኦሞ ዞን ውስጥ ይኖራሉ፡፡ ዞኑ በ8 ወረዳዎች እና 1 የከተማ አስተዳደር የተከፈለ ሲሆን ከነዚህ ወረዳዎች “ቀይ አፈር” የተባለች አነስተኛ ከተማን መናገሻቸው አድርገው የሚናሩት የበና፤ ፀማይ እና ብራይሌ ብሔሮች ወረዳ የሆነችው የበና ፀማይ ወረዳ አንዷ ነች፡፡
በወረዳው የበና እና ፀማይ ብሔሮች ከፍተኛውን ቁጥር የያዙ ሲሆን ብራይሌዎች በአንፃሩ በመጥፋት ስጋት ላይ ያሉ ብሔሮች ናቸው፡፡ በአሁኑ ሰአት 61 የብራይሌ ብሔር አባላት ብቻ ሲኖሩ አንጐታ የተባለውን ቋንቋቸውን መናገር የሚችሉት 12 ያህል ብቻ ናቸው፡፡
የብሔረሰቡ አባላት በወረዳው በእንጨቴ ቀበሌ በልዩ ስሙ ገኤ ወንዝ፣ ድሮ ነው በሚባል መንደር ተሰባስበው የሚኖሩ ሲሆን፤ አንድም የብሔረሰቡ አባል ከተጠቀሰው መንደር ውጪ በየትኛውም ስፍራ አይገኝም፡፡
ብሔረሰቡ የተመሠረተበት ምክንያት በተለያዩ አካባቢዎች ድርቅና ረሃብ በመከሰቱ በምግብ ፍለጋ ስምሪት ሲሆን፤ ከሰባት ከማያንሱ ብሄረሰቦች ተሰባስበው የተመሠረተ ነው፡፡ እነዚህም ኮንሶ፣ ገዋዳ፣ ማሌ፣ ቦና፣ ጋቦ፣ ቦረና እና ኤርቦሬ ናቸው፡፡ ለብሔረሰቡ ቁጥር ማነስ ዋነኛ ምክንያቶች ተብለው ከሚጠቀሱት መካከል በአካባቢው የትምህርትና የጤና ተቋማት በበቂ ሁኔታ አለመገንባታቸው፣ በበረሃማው የአየር ንብረት ምክንያት በሚፈጠሩ መርዛማ እባቦች ተነድፎ መሞት እንዲሁም በከፍተኛ ሁኔታ በወባ ወረርሽኝ እና በሌሎች የጤና እክሎች መጠቃት ይገኙባቸዋል እንደ ወረዳው የባህልና ቱሪዝም የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት መረጃ፡፡
በመጥፋት ላይ ያለው ይህ ብሔረሰብ 3 ባህላዊ የአስተዳደር እርከኖች አሉት፡፡ የበላይ ሆኖ የሚያስተዳድረውና 5 አባላት ያሉት “ባልኮ” ሲሰኝ፣ በተመሳሳይ 5 አባላትን ያቀፈውና የምክትል አስተዳዳሪነት ስልጣን ያለው አካል ደግሞ “ሙርጃል አፍ” ይሰኛል፡፡ “ሙርጃል አፍ” ዋነኛ ሃላፊነቱ በብሔረሰቡ መካከል ችግሮች ሲፈጠሩ ይፈታል፣ ስብሰባዎች ሲኖሩ ባህላዊ መጠጥ (ጨቃ) እንዲዘጋጅ ትዕዛዝ ያስተላልፋል። ሶስተኛው የአስተዳደር እርከን እንደቀደሙት ሁሉ 5 አባላትን ያቀፈ ሲሆን “ጉርማልኮ” ይሰኛል፡፡ የዚህ ደረጃ ባለስልጣን መሆኑን ለመለየት “ዘንግ” ይይዛል፡፡ ዘንጉን የያዙት የሚሰበሰቡበት ሜዳ ላይ ሴቶች ድርሽ ማለት አይፈቀድላቸውም፡፡ የሜዳው ስም ናቦ ይባላል፡፡
ብራይሌዎች ሶስት የጋብቻ አይነቶች አሏቸው፡፡ የመጀመያው “ኢፋም” የተሰኘ ሲሆን በሁለቱ ተጋቢዎች ስምምነት የሚፈፀም ነው፡፡ “አይሳት ሻዳል ቤት” የተሰኘው ጋብቻ ደግሞ የውርስ ጋብቻ ነው፡፡
“እዴ ባዶጂካ ኢስማ” ደግሞ በተጋቢ ወላጆች ስምምነት የሚፈፀም ጋብቻ ነው፡፡ ወንዱ ለአቅመ አዳም በሚደርስበት ወቅት በሴቷ ጥሎሽ የሚሰጠው አሣ፣ ማርና ጋቢ ነው፡፡ በብሔረሰቡ የወንድም ሆነ የሴት ግርዛት ነውር ነው፡፡
በብራይሌዎች ዘንድ በለቅሶ ወይም ሃዘን ወቅት ለልጅና ለአዋቂ የሚከወነው ስርአት የተለያየ ነው፡፡ አዋቂ ሲሞት አረቄ ተገዝቶ፣ ባህላዊ መጠጥ (ጨቃ) እየተጠጣ ይጨፈራል፣ መሣሪያ ይተኮሳል፣ የሟች ደግ ስራ በዘፈን ይወደሳል፡፡
ይህ ስርአት እየተከወነ አንድ ቀን ይታደርና ቀጥሎ ባለው ቀን ግብአተ መሬቱ ይፈፀማል፡፡ ወጣት ወይም ልጅ ከሞተ ደግሞ እጅግ ይታዘናል፡፡ አምርረው ያለቅሳሉ። የቡና ገለባ (ሸፈሮ ይባላል) አፍልተው ይጠጣሉ፣ ሃዘናቸውን ለመግለጽም አምባር፣ ጨሌና ሌሎችንም ጌጣጌጦቻቸውን ያወልቃሉ፤ ፀጉራቸውንም ይላጫሉ፡፡
ብራይሌዎች በስፋት ለምግብነት የሚጠቀሙት አሣ ነው፡፡ በአካባቢው ከሚገኘው የወይጦ ወንዝ አሣ በማውጣት፣ የአሣውን ስጋ እንደ ቋንጣ በመዘልዘል ይመገቡታል፡፡ ሙዝ፣ በርበሬና ሽንኩርት ይተክላሉ፡፡ በባህላዊ ቀፎ ንብ በማርባት በሚያገኙት የማር ምርትም ይታወቃሉ፡፡

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ስሙኝማ…አንድ በጣም የቸገረን ነገር አለ…ለምንድነው ሁልጊዜ ወጥተንም፣ ወርደንም ሌላው ሰው ያደረገውን እኛም ማድረግ የምንፈልገው! አይገርማችሁም! ፉክክር አይሉት፣ መንፈሳዊ ቅናት አይሉት፣ ጤናማ ውድድር አይሉት…ያኛው ስላደረገው ብቻ ሌሎቻችን ‘ኮፒ ፔስት’ ለማድረግ ስንሽቀዳደም የምር ቀሺም ነገር ነው፡፡
አንድ ወዳጄ የነገረኝን አባባል ስሙኝማ…“ባለ እንጨት ስትጥል አይታ፣ ባለ እንስራዋም ጣለች…” እንስራው ሲከሰከስ አስቡትማ! አሀ…ያቺኛዋ ጥላለቻ! “ጓደኛዋ ጥላ እሷ አንከርፍፋ መጣች…” የምትባል ይመስላታላ! ኮሚክ ነገር እኮ ነው…“ማን ጥሎ ማን ይቀራል!” አይነት ነገር ነው የሚመስለው!
እኔ የምለው… አንዳንድ የሬድዮ ፕሮግራሞችን ነገሬ ብላችሁልኛል! ምን አለፋችሁ… እንጨት ሲጥሉ አይቶ እንስራ… ነገር በሽ በሽ ነው፡፡ አንዱ ፕሮግራም ሞክሮት ጥሩ አድማጭ ያገኘ የሚመስለውን አቀራራብ ሌሎች ‘ኮፒ ፔስት’ ለማድረግ ሲሞክሩ ትሰማላችሁ፣ ታያላችሁ፡፡ ኮሚኩ ነገር እኮ ምን መሰላችሁ… አንዳንዴ ‘ኮፒ ፔስት’ ሲደረግ የድምጽ ቅላጼው እንኳን አይቀርም!  
ስሙኝማ..እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ማስታወቂያዎች ላይ በተለይ እንዲሀ አይነት ነገር ደጋግማችሁ ታያላችሁ (‘ቤት አመታት’ ሳይቀር..ቂ..ቂ..ቂ…)፡፡  
“ባለ እንጨት ስትጥል አይታ፣ ባለ እንስራዋም ጣለች…” አሉ፡፡
ስሙኝማ…የአባባል ነገር ካነሳን አይቀር…አንድ ሚኒባስ ታክሲ ላይ ምን የምትል አባባል አለች መሰላችሁ…“ክፉ ቀንና ጥይትን ዝቅ ብሎ ማሳለፍ ነው፡፡” ሚኒባሶች “እንደ ቤትሽ አትንጣጪ” “ዝቅተኝነት ከተሰማህ፣ ዛፍ ላይ ውጣ…” አይነት እየለጠፉ እንደሚያበሽቁን ሁሉ፣ እንደዚችኛዋ አይነት አሪፍ አባባሎች አልፎ አልፎ ታገኘላችሁ፡፡
ነገርዬውማ… ክፉ ቀንን ዝቅ ብሎ ማሳለፍ አሪፍ ነው፡፡ ችግሩ ምን መሰላችሁ… እዚች እኛይቱ አገር አንድን እንቅልፍ ያሳጣችሁን ችግር “ዝቅ ብዬ አሳለፍኩት…” ስትሉ ነገርዬው በየትም፣ በየትም ዞሮ ይመጣና ከምድር ውስጥ ፈልፍሎ ይወጣላችኋል፡፡ እናም ማምለጫ መንገዱም አስቸጋሪ እየሆነ ነው፡፡
እናላችሁ…“ባለ እንጨት ስትጥል አይታ፣ ባለ እንስራዋም ጣለች…” አሪፍ፣ ለእኛ በልክ የተሰፋች አባባል ትመስላላች፡፡
ልክ ነዋ…አገር እንኳን ‘እንጨት ሲጥሉ አይታ እንስራ የምትጥል…’ ትመስላለች፡፡ “እነእንትና እንዳደረጉት…” “እንትን አገር ተሞክሮ ስኬታማ የሆነ…” ተብሎ ይጫንላችኋል፡፡ ታዲያላችሁ… እንኳን እኛ ዘንድ ስኬታማ ሊሆን ቀርቶ… አለ አይደል… ነገርዬው ሁሉ ‘እንጨት ሲጥሉ ታይቶ እንስራ መጣል’ ይሆናል፡፡
ስሙኝማ… እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ማህጸንም ለ‘ማከራየት’ ደረስን አይደል! እናላችሁ… ስለ ማህጸን ኪራይ ስታነቡ “ምነው ይሄ ‘ማከራየት’ የሚሉት ነገር ለሌላ ሁሉ ቢሠራ…” ያስብላችኋል!
ልክ ነዋ…ለምሳሌ ‘ቦተሊከኞቻችን’ ህዝብን ፊት የመናገር ጥበብን ከሰለጠኑት ‘ይከራዩልን’፡፡ አሀ… “ሁልህም አናውቅህምና ነው… ሱሪህን ሁሉ በቀበቶ መታጠቅ የጀመርከው ዕድሜ ለእኛ በል!” “ውስጥ ለውስጥ የምትጎነጉኑትን የማናውቅ መሰላችሁ…” አይነት የፊት ለፊትና ‘የሾርኒ’ ንግግር ሰለቸና!  የምር እኮ ብዙ “ፖለቲካ ከእኛ በላይ ላሳር!”፣ “አገር መውደድ ከእኛ በላይ ላሳር!” “አዋቂ ከእኛ በላይ ላሳር!”፣ የሚሉ በሁሉም ወገን ያሉ የዘመናችን ሰዎች የኪራይ አእምሮ ቢያገኙ አሪፍ ነበር፡፡ የምር እኮ…. ፊት ለፊታቸው ማይክ በቀረበ ቁጥር አርጩሜ የያዙ ‘ክፉ የኔታ’ መሆን የሚቃጣቸው መአት አለሉላችሁ፡፡
‘የአእምሮ ኪራይ’ የሚባል ነገር ይጀመርልንማ። አሀ… አንዱ ችግራችን እዛ ላይ ነዋ!… ከፍ ብለን የጠቀስነውን አይነት… “ከእነእንትና የቀዳነው ህግ…”፣  “ከእነእንትና ባገኘነው ተሞክሮ…” ምናምን ከማለት አንደኛውን አእምሯቸውን ‘ያከራዩን’ና እኛው ‘እንፍጠራ’!
ፈራንካ ባይኖረንም በምግብ ለሥራም ቢሆን እንከፍላለና! ያው ብድር ስናበዛ “የሰጠናችሁን ብድር ቁጭ አድርጓት…” ማለታቸው ባይቀርም… የሆነ ነገር፣ ወይ የውሀ ጉድጓድ፣ ወይ ተቆፍሮ የሚወጣ ነገርዬ ያለበት ቦታ ሰጥተን አፋቸውን እናሲዛለና! እንኳንም ለወዳጅ የሚሆን ጉድጓድ አላሳጣንማ!
“አእምሮ ለመከራየት የወጣ ዓለም አቀፍ ጨረታ፡፡ መስፈርቶቹ የሚመረጠው አእምሮ ከኔኦሊበራሊስቶች፣ ናፋቂዎች፣ አተራማሾች፣ ምንምን ንክኪ እንደሌለው የሚያረጋግጥ ሰርተፊኬት ከቤይጂንግ ወይም ከሻንጋይ ክሊኒክ ማምጣት ይኖርበታል፡፡” አሪፍ አይደል! ሀርቫርድ፣ ኦክስፎርድ ጅኒ ጅቡቲ ብሎ ነገር የለም፡፡ ቤይጂንግና ሻንጋይ ብቻ! (ስሙኝማ…መቼ ነው ወዳጆቻችን ቤይጂንግ ህንጻ ስር መኪና ተደግፈው “መኪናዬን ተደግፌ በምኖርበት አፓርተመንት ስር…” ምናምን የሚል የተጻፈበት ፎቶ መላክ የሚጀምሩት! እዛ ፓርኪንግ ሥራ የለም እንዴ! ቂ…ቂ…ቂ…
ምን አለ በሉኝ፣ ነገራችን ሁሉ “ባለ እንጨት ስትጥል አይታ፣ ባለ እንስራዋም ጣለች…” አይነት ስለሆነ ሁለት ሰው እንደዛ አይነት ፎቶ በላከ ማግስት ሁለት ሺህ ሰው ይልካል፡፡ (እግረ መንገዴን…ጓዳኞቻቸው “አወጣኋት…” የሚሏትን እንትናዬ ሁሉ የሚያሳድዱ ሰዎች ገጥመዋችሁ አያውቁም! እንደ ጀግንነት ይቆጥሩታል መሰለኝ፡፡)
“የሚጠቅሱ ሴቶች በዝተዋል…” ያልከኝ ወዳጄ በግራ ነው በቀኝ ዓይናቸው የሚጠቅሱት? አሀ… በቀኝ ከሆነ ቀኝ አክራሪ ሊሆኑ ስለሚችሉ እንጠነቀቃለና! ልጄ… አውሮፓ ሁሉ ቀኝ፣ ቀኝ እያለ ስለሆነ ‘መጥኔ ለመጤ’ እያልን ነው፡፡
ሴቶችን ለጥቅሻ ያበቃህ አንድዬ በቀን አምስቴ እንቆቆ የሚጠጡ የሚመስሉ ቦሳቻችንን ፈታ አድርጋቸውማ! ቢደብሩንም እንኳን ትንሽ እኛን መስለው ቢደብሩን ይሻላል፡፡
ስሙኝማ…ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…አንድ ካፌ ውስጥ “ከ30 ደቂቃ በላይ ቁጭ ብሎ ጋዜጣ ማንበብ ክልክል ነው፣” የሚል ማስታወቂያ ተለጥፏል፡፡ እንዴት ቢቸግራቸው እንደሆነ አይታያችሁም! ኮሚክ እኮ ነው፣ አንዳንዶቻችን በአንድ ማኪያቶ አምስት ጋዜጣ ካላነበብንና ሌሎች ስምንት ዘጠኝ መጽሔቶች ካላገላበጥን በስተቀር ‘ወንበር አንለቅም’፡፡ አይደለም የንግድ ቤት የዘመድ ቤት እንኳን ምሳ ሰዓት አልፈን እስከ መክሰስ ከቆየን እኮ ፊታቸውን ትንሽ ጠቆር ማድረጋቸው አይቀርም። ሲበዛም አሪፍ አይደለማ! እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ምን ይመስለኛል መሰላችሁ… ሬስቱራንቶቹ አንደኛውን “ጋዜጣ ማንበብ አይፈቀድም” ብለው ቢለጥፉ ሊደርስባቸው የሚችለውን እያሰቡ የሚተዉት ይመስለኛል፡፡ እኛም “ስሙኝማ…” ማለታችን አይቀርማ!
አሁን፣ አሁን አንዳንድ ቤቶች “ላፕቶፕ መጠቀም ክልክል ነው…” እያሉ መለጠፍ ጀምረዋል። ምን ይደረግ! አንዳንዱ ላፕቶፑን ሶኬት ላይ ይሰካና ለአንድ ሻይና ለአንድ ቦምቦሊኖ ሬስቱራንቱን ቢሮው ያደርገዋል፡፡ ሦስት ሰዓት ገብቶ ሰባት ሰዓት ይወጣላችኋል፡፡ እስከዛ ድረስ እኮ የጥበቃ ሠራተኞች ሺፍት እንኳም ተለውጦ ሊሆን ይችላል፡፡
አንድ ሬስቱራንት ደግሞ… “ከተገለገሉ በኋላ ለሌላ ተገልጋይ ቦታውን ይልቀቁ፣” የምትል ማስታወቂያ አለች፡፡ የምር ግን እኮ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል፣ ብዙዎቻችን ይቺን ታክል ይሉኝታ እያጣን እኮ ነው! የአራት ብር ሻይ አዘን አራት ሰዓት ሙሉ ተደላድለን እንቀመጣለን፡፡ ለንግድ የተቋቋመም ሬስቱራንትን ብሔረ ጽጌ መናፈሻ አይነት ማድረግ ልክ አይደለም!
እኔ የምለው…‘እዛ ቦታ’… አለ አይደል…በር ተንኳኩቶ “ሰዓት ሞልቷል…” ስንባል ወይ እንወጣለን ወይ ጮክ ብለን “እጨምራለሁ!” እንላለን፡፡ ያውም ‘መጮህ’ ከተቻለ!  አሀ… ልጄ ‘አንዳንድ ነገሮች’ እኮ ድምፃችንን ያጠፉና በ‘ትንፋሽ ብቻ’ ይተኩታል! ቂ…ቂ…ቂ…
እናላችሁ…“ባለ እንጨት ስትጥል አይታ፣ ባለ እንስራዋም ጣለች…” አይነት አስተሳሰብ ራሳችንን እንዳንሆን እያደረገን ነው፡፡
እንጨቱም፣ እንስራውም አይውደቁማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል
Saturday, 21 June 2014 14:23

የፖለቲካ ጥግ

ምንም ዝግጅት አያስፈልገውም ተብሎ የሚታሰብ ብቸኛው ሙያ፣ ፖለቲካ ሳይሆን አይቀርም፡፡
ሮበርት ሉዊስ ስቲቨንሰን
ፖለቲካ፤ ሰዎች በትክክል በሚመለከቷቸው ጉዳዮች ላይ እንዳይሳተፉ የመከልከል ጥበብ ነው፡፡
ፓውል ቫለሪ
አልፎ አልፎ ሁሉንም ሰው ልታሞኝ ትችላለህ፡፡
አንዳንዱን ሰው ሁልጊዜም ልታሞኘው ትችላለህ።
ሁሉንም ሰው ግን ሁልጊዜ ልታሞኘው አትችልም፡፡
አብርሃም ሊንከን
አገርን በትክክል መምራት የሚያውቁበት ሰዎች በታክሲ ሹፌርነትና በፀጉር አስተካካይነት ሥራ መጠመዳቸው በእጅጉ ያሳዝናል፡፡
ጆርጅ በርንስ
ፖለቲከኞች የትም ዓለም ላይ አንድ ናቸው፡፡ ወንዝ በሌለበትም ጭምር ድልድይ እንሰራለን ብለው ቃል ይገባሉ፡፡
ኒኪታ ክሩስቼቭ
ፖለቲካ ከፊዚክስ የበለጠ አስቸጋሪ ነው፡፡
አልበርት አንስታይን

ቀለም የዘለቃቸው ዋሾዎች ከፖለቲከኞችም ይብሳሉ ተባለ!

           ባለፈው ሳምንት የአብዛኞቹ ሚዲያዎቻችን ሰበር ዜና የሆኑት ግለሰብ ለዚህ “ልዩ ጽሑፍ” መሰናዳት ሰበብ እንደሆኑኝ ለመግለጽ እወዳለሁ፡፡(እውነቱን መናገር ይሻላል ብዬ እኮ ነው!) ምስጋናውን ለማን ማቅረብ እንዳለብኝ ግን እርግጠኛ ስላልሆንኩ ለጊዜው “የምስጋና ማዕቀብ” ማድረጉን መርጬአለሁ፡፡ እናም በቀጥታ ወደ ርዕሰ ጉዳያችን እንግባ፡፡ ዛሬ አምዱ ለዋሾዎች ተለቋል (ድሮስ የማን ነበር አትሉኝም?)
ባለፈው ቅዳሜና እሁድ ምን ሰማሁ መሰላችሁ? እኚህ የትምህርት መረጃቸውን አስመልክቶ ዋሽተዋል የተባሉት ግለሰብ እንግዲህ አነቃቂ ንግግሮችን በማድረግ ይታወቃሉ አሉ ?! እናላችሁ ---- በሳቸው የማነቃቂያ ንግግር ተነሳስተው ለውጥ ያመጡ አንዳንድ ግለሰቦች በጣም ተናደዱ ተባለ፡፡ ለምን መሰላችሁ? የውሸት አነቃቅቶናል ብለው እኮ ነው። እኔ የምለው ---- “ፌክ ማነቃቂያ” አለ እንዴ? (“የወደቀ ዛፍ ምሳር ይበዛበታል” አሉ!) እንግዲህ በውሸት ማነቃቂያ ተነቃቅተን ነበር ያሉትን ሰዎች ወደቀድሞው “እንቅልፋቸው” መመለስ ከባድ ይመስለኛል፡፡ (የቀድሞ እንቅልፋቸውን ከፈለጉ ማለቴ ነው!)
እኔማ ምስኪኑ ከባባድ ውሸቶችን የሚዳፈሩት ፖለቲከኞች ብቻ ይመስሉኝ ነበር፡፡ ለካስ የቀለም ቀንድ የሚባሉትም ሳይቀሩ ድብን አድርገው ይዋሻሉና! (ተምሮ ውሸት አይደብርም?) ሰሞኑን ታዲያ በዋሾነት ዙሪያ የተደረጉ ጥናቶችን ሳነብላችሁ ነበር (“የቸገረው እርጉዝ ያገባል” አሉ!) እናላችሁ…ባለ ከባድ ሚዛን ዋሾዎች ሲገጥሟችሁ ነገርየውን የሞራል ጉዳይ ብቻ አድርጋችሁ አትመልከቱት፡፡ ጉዳዩ ህክምና የሚሻ በሽታ ወይም አደገኛ ሱስ  ነው ይላሉ - አጥኚዎቹ፡፡
መቼም ዋሾነትን በተመለከተ የሰለጠኑት አገራት ተመክሮ ምን እንደሚመስል መቃኘት ተገቢ ይመስለኛል፡፡ ለውድድርና ለንፅፅር ብቻ ሳይሆን ግንዛቤን ለማስፋትም ያግዛል፡፡ እናላችሁ---- ከኢንተርኔት ያገኘኋቸው በርካታ አስገራሚ መረጃዎች እንኳን ለእኔ ለናንተም የሚተርፍ ነው። (ለካ የሰለጠኑትም  ይዋሻሉ!) አሁን በቀጥታ የሰለጠኑ አገራትን የዋሾነት ተመክሮ ወደመቃኘቱ እንግባ፡፡ (የፅሁፉ ዓላማ መረጃ ማቀበል  እንደሆነ ይታወቅልኝ!) ከታላቋ እንግሊዝ እንጀምር። (እንግሊዝ የታሪኩ መቼት እንጂ ባለቤት አይደለችም!)
  እንግሊዛዊው የዝነኞች ሼፍ ሮበርት አይርቪንግ እ.ኤ.አ በ2008 ዓ.ም ከገዛ ራሱ የምግብ ዝግጅት የቴሌቪዥን ሾው የተባረረው በሌላ ሳይሆን በዋሾነቱ ነበር፡፡ ይሄ ዓለምአቀፍ ሼፍ ምን ቢዋሽ ጥሩ ነው? “የልኡል ቻርልስና የልዕልት ዲያናን የሰርግ ኬክ የሰራሁት እኔ ነኝ” ብሎ ማውራት ማስወራት ጀመረ፡፡ (ያለዕዳው ዘማች አሉ!) የማታ ማታ ታዲያ የልኡሉንና የልእልቷን ኬክ የሰራው ሌላ ሼፍ መሆኑ በመረጋገጡ አይርቪንግ ቅሌት ተከናነበ፡፡ ኬኩ በተሰራበት ት/ቤት ተገኝቶ ከመመልከት ባሻገር ለኬኩ ማስጊያጫ የሚሆኑ ፍራፍሬዎችን ያቀረበ ቢሆንም ፈፅሞ ኬኩን በመስራት አልተሳተፈም ነበር፡፡ ተዋረድ ሲለው ግን እኔ ነኝ የሰራሁት እያለ “ሲሰጥ” ከረመ (ሳይቸግር ጤፍ ብድር አሉ!)
አሁን ደግሞ ወደ አማሪካ መጥተናል፡፡ ማሪል ጆንስ በማሳቹሴትስ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ኮሌጅ ውስጥ ለ28 ዓመታት በዲንነት ያገለገለች ስትሆን መጀመርያ ስትቀጠር የባችለር ድግሪና ማስተርስ አለኝ ብላ ማመልከቻዋ ላይ ጽፋ ነበር፡፡ በመጨረሻ ግን ጆንስ  የኮሌጅ ድግሪ የሚባል ነገር ፈጽሞ እንደሌላት ይፋ ሆነ፡፡ (“አበስ ገበርኩ” ማለት ይሄኔ ነው!) ዋሾነቷ ያተረፈላት ነገር ታዲያ በውርደት ከስራ መባረርን ብቻ ነው፡፡ (ሰው 28 ዓመት ሙሉ ይዋሻል?)
ጆንስ በ2007 ዓ.ም ሥራዋን ስትለቅ በዩኒቨርስቲው ድረገጽ ላይ ባሰፈረችው ጽሑፍ፤ የትምህርት ማስረጃዎቿን በተመለከተ ለተቋሙ የተሳሳተ መረጃ ማቅረቧን ጠቁማ፣  ያኔ ለሥራ ስታመለክትም ሆነ ከዚያ በኋላ በነበሩት ጊዜያት የትምህርት ማስረጃዎቿን የማስተካከል ወኔ እንዳልነበራት ተናግራለች (የምን ወኔ ነው የምታወራው?!) አሁን ማሪል ጆንስ፤ በበርክሌይ ኮሌጅ ኦፍ ሚዩዚክ የተማሪዎች ቅበላ አማካሪ ሆና እየሰራች ትገኛለች፡፡ (ውሸት አያስከስስም እንዴ?)
የIBM ሶፍትዌርን የሚሰራው “ሎተስ ዴቨሎፕመንት” ፕሬዚዳንት ጄፍሬይ ፓፖስ ስለትምህርቱና የውትድርና ታሪኩ የተናገረው ሁሉ ቅጥፈት መሆኑ የታወቀው ዘግይቶ ነው፡፡ ፓፖስ ፓይለት ነበርኩ ቢልም የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪ ሆኖ የተገኘ ሲሆን የባህር ሃይል መቶ አለቃነቱንም በሻምበልነት ሽሮ ነው ሥራ የተቀጠረው፡፡ ይሄ ብቻ ቢሆን ጥሩ ነበር፡፡ ፒኤችዲውን ከፔፕርዲን ዩኒቨርሲቲ መቀበሉንም ለቀጣሪዎቹ ዋሽቶ ነበር፡፡ እውነቱ ሲወጣ ግን ፒኤችዲውን ያገኘው ዕውቅና ከሌለው የተልዕኮ ት/ቤት እንደሆነ ተጋለጠ።  ጄፍሬይ ፓፖስ ይሄን ሁሉ ቢዋሽም ከስራው አልተባበረም ነበር፡፡ ሆኖም ብዙም አልቆየ፡፡ የፆታ መድልዎ ፈጽሟል በሚል በቀረበበት ቅሬታ ሥራውን ለቀቀ። አሁን የMaptu Corp. and weblayers inc. ዋና ሥራ አስፈፃሚ በመሆን እየሰራ ይገኛል፡፡
በአንድ ወቅት የ”ሳሎሞን ስሚዝ ባርኔይ” ተቀጣሪ የነበረው ጃክ ግሩብማን፤ የዎልስትሪት ከፍተኛ ተከፋይ አናሊስት ነበር፡፡ በዓመት 20 ሚ. ዶላር የሚከፈለው (በወር ከ1.5 ሚ.ብር በላይ ማለት ነው) ጉድና ጅራት ከወደ ኋላ ነው እንዲሉ ግን፣መጨረሻ ላይ የተማረበትን ዩኒቨርሲቲ በተመለከተ መዋሸቱ ታወቀበት፡፡  እሱ እንዳለው፤ ከማሳቹሴትስ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ኮሌጅ አልነበረም የተመረቀው፡፡ ከቦስተን ዩኒቨርሲቲ እንጂ፡፡ (እንደ እኛ አገር ዋናው መመረቁ ነው ተብሎ አልታለፈም!)
ግሩብማን ውሸቱ መጋለጡን ተከትሎ ለቢዝነስ ዊክ በሰጠው ቃለምልልስ፤ የዋሸው የሥራ ደህንነት ስጋት ተሰምቶት ሳይሆን እንደማይቀር ተናግሯል። (የሥነ ልቦና ባለሙያዎች ግን የግብረገብነት ችግር ነው ባይ ናቸው!)
አሁን ግሩብማን፤ ለቴሌኮምና ለቴክኖሎጂ ኩባንያዎች የምክር አገልግሎት የሚሰጥ Magee Group የተባለ ኩባንያ አቋቁሞ እየሰራ ይገኛል፡፡ (አሁንስ እንመነው?)  የቀድሞ የያሁ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ስኮት ቶምፕሰን፤ መጀመሪያ የተቀጠረው በአነስተኛ የስራ መደብ ስለነበር፣ የትምህርት ማስረጃዎቹን በተመለከተ ነገሬ ብሎ የመረመረው አልነበረም። እሱም ታዲያ ተመቸኝ ብሎ በደንብ ዋሸ፡፡ ከስቶንሂል ኮሌጅ በአካውንቲንግና በኮምፒዩተር ሳይንስ ሁለት ዲግሪዎች ተቀብያለሁ በማለት፡፡
የቀድሞው “paypal” ፕሬዚዳንት ቶምፕሰን፤ በጃንዋሪ 2012 ዓ.ም የያሁ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሆኖ ሲሾም ነው ከዓመታት በፊት በገዛ እጁ የቀበረው ፈንጂ የፈነዳው፡፡ የያሁ ባለድርሻ የሆነው ዳንኤል ኤስ. ሎብ መረጃ ከየት እንዳገኘ ባይታወቅም የቶምፕሰንን የትምህርት ታሪክ ይፈትሽ ገባ። በመጨረሻም አዲሱ ሥራ አስፈፃሚ ቶምፕሰን በአካውንቲንግ እንጂ በኮምፒዩተር ሳይንስ ድግሪ እንደሌለው አረጋገጠ። የቶምፕሰንን ዋሾነት በመንቀፍ አስተያየቱን የሰጠው ዳንኤል ኤስ ሎብ፤ “አሁን ከመቼውም ጊዜ የበለጠ የያሁ ኢንቨስተሮች እምነት የሚጥሉበት ዋና ስራ አስፈፃሚ የሚያስፈልጋቸው ሰዓት ነው” ሲል የተናገረ ቢሆንም ለጊዜውም ቢሆን ዋና ሥራ አስፈፃሚው ይሄ ነው የሚባል እርምጃ አልተወሰደበትም፡፡  
የያሁ ሥራ አስፈፃሚ በዋሾነቱ የተነሳ ከስራው ባይባረርም፣ ከኃላፊነቱ ባይነሳም፣ የደሞዙ መጠን ባይቀነስም… ከሃፍረትና ከመሸማቀቅ እንደማይድን ቀጣሪዎቹ ነግረውት ነበር፡፡ (የዋሾነት ደሞዙ ሃፍረትና መሸማቀቅ ነው እንደማለት!) በነገራችሁ ላይ የእነዚህ ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች የትምህርት ማስረጃ ማጭበርበር ጉዳይ አንድ ሰሞን የአሜሪካ ጋዜጦች ዋነኛ ርዕሰ ጉዳይ ሆኖ ነበር፡፡ (አንዱ ድግሪ የእውነት፣ ሌላኛው ድግሪ የውሸት እየሆነ አስቸገራቸዋ!)
ኬኔዝ ሎንቻር፤ “ቨሪታስ” የተባለውን ትልቁን የሶፍትዌር ኩባንያ የተቀላቀለው በ1997 ዓ.ም ነበር። ከአራት ዓመት በኋላ የውጭ ባለድርሻ አካላትን ውጤታማ በሆነ መንገድ በመምራት “CFo Magazine’s Excellence Award” አሸነፈ። በቀጣዩ ዓመት ግን ትከሻው ላይ የተደረበለትን የስኬት ፀጋ ተገፈፈ። ለምን ቢሉ? ከስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲ አግኝቻለሁ ያለው MBA የውሸት መሆኑ በመረጋገጡ ነው። ከአሪዞና ስቴት ዩኒቨርሲቲ ተቀብያለሁ ያለውም የአካውንቲንግ ድግሪ ቅጥፈት ነው ተባለ፡፡ እሱ ድግሪውን ያገኘው ከአይዳሆ ዩኒቨርስቲ ነበር። ይሄንን ተከትሎም የኩባንያው የስቶክ ዋጋ በ20 በመቶ አሽቆለቆለ፡፡ ከዚያም ሎንቻር በኩባንያው የተዘጋጀለትን መግለጫ ሰጥቶ  ሥራውን እንዲለቅ ተጠየቀ፡፡
“በዚህ የተሳሳተ የትምህርት ማስረጃዬ አዝናለሁ። አሁን ባለው ሁኔታ ሥራዬን መልቀቄ ለእኔም ሆነ ለኩባንያው ጥቅም ይበጃል ብዬ አምናለሁ” ሲል ሚ/ር ኬኔዝ ሎንቻር የስንብት መግለጫውን ሰጥቷል።
በ1994 ዓ.ም “ሬዲዮ ሻክ”ን የተቀላቀለው ዴቪድ ኤድመንድሰን፤ የኩባንያውን የዕድገት መሰላል በከፍተኛ ፍጥነት ተወጣጥቶ፣ በ2005 ዓ.ም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ለመሆን በቅቷል፡፡ አዲሱን ሹመት ባገኘ በዓመቱ ግን “ፎርዝ ዎርዝ ስታር ቴሌግራም” የተሰኘው ጋዜጣ አንድ ውሸት አጋለጠ፡፡ ኤድመንድሰን ሥራውን ሲቀጠር እንደገለፀው፤ (እንደዋሸው ቢባል ይሻላል!) ከ “ኸርትላንድ ባፕቲስት ባይብል ኮሌጅ” በሥነ መለኮትና በሥነልቦና ድግሪውን አለማግኘቱን አረጋግጫለሁ አለ - ጋዜጣው፡፡  የሬዲዮ ሻክ የዳይሬክተሮች ቦርድ ዋና ሥራ አስፈፃሚው ከስራው እንዲባረር ባይፈልጉም ኤድመንድሰን ግን ሥራውን ለመልቀቅ ቅንጣት አላቅማማም፡፡ (ሃፍረቱ እንዴ ያሰራው?) “የትምህርቴን ጉዳይ በተመለከተ የተዛባ መረጃ  አቅርቤአለሁ፤ ለዚህ መዛባት ተጠያቂው እኔ ብቻ ነኝ። አሁን የሥነመለኮት ዲፕሎማ ማቅረብ እንደማልችል አውቃለሁ” ብሏል - ከመልቀቁ በፊት በሰጠው መግለጫ፡፡
የዓይን ጤና መጠበቅያ ምርቶችን የሚያቀርበው “Bausch and Lomb” የተሰኘው ኩባንያ የቀድሞ  ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሮናልድ ዛሬላም የዋሾነት ሰለባ ከመሆን አልዳኑም፡፡ እሳቸው ደግሞ ከኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ ኤምቢኤዬን ተቀብያለሁ በማለት ነው የዋሹት፡፡ በእርግጥ ትምህርቱን ጀምረውት ነበር፤ ሆኖም ዳር ሳያደርሱት ማቋረጣቸውን ዩኒቨርስቲው ጠቁሟል፡፡ እናም ለዚህ ዋሾነታቸው የ1 ሚሊዮን ዶላር ቦነሳቸውን አጥተዋል፡፡ ሥራቸውን ግን አላጡም፡፡ “ለኩባንያው በጣም አስፈላጊ ናቸው” ተብለው በሃላፊነታቸው ሊቀጥሉ ችለዋል፡፡ የማታ የማታ ግን (በ2008 ዓ.ም) ኩባንያው እጅግ በርካታ የታዘዙ ምርቶቹ ተመላሽ ሲሆኑና በፍ/ቤት ክስ ሲጨናነቅ ዛሬላም ጥለውት ውልቅ አሉ፡፡
የኖርዌይ ተወላጇ ሊቭ ሎበርግ፤ በፍ/ቤት ተከስሳ ጥፋተኝነቷ ከመረጋገጡ በፊት፣ ለበርካታ ዓመታት በጤና እንክብካቤ ዘርፍና በሌሎች የመንግስት ተቋማት በከፍተኛ የአስተዳደር ቦታዎች ላይ ተመድባ ስታገለግል ቆይታለች፡፡ (በአገሯ ኖርዌይ ማለት ነው!) በኖርዌይ የፕሮግረስ ፓርቲ ውስጥም በፖለቲከኛነት ተሳትፋለች፡፡ (ውሸት ለፖለቲከኛ ብርቁ አይደለም!)
በ2010 ዓ.ም ነው አንድ ጋዜጠኛ እውነቱን ያፍረጠረጠባት፡፡ ከለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ፣ ከኩዊን ሜሪ ኮሌጅና ከኖርጅስ ሃንድልሾይስኮሌ አግኝቻለሁ ያለቻቸው ድግሪዎች በሙሉ የውሸት እንደሆኑ ጋዜጠኛው አጋልጧል፡፡ ሌላው ቀርቶ በመንግስት የብቃት ማረጋገጫ የተሰጣት (Certified) ነርስ እንደሆነች ስትናገር የከረመችው ሁሉ ቅጥፈት መሆኑ ተነገረ፡፡ ሎበርግ፤ እንኳንስ ኮሌጅ ልትገባ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን እንኳን አላጠናቀቀችም ነው የተባለው፡፡ የነርስ ትምህርቷም የአንድ ዓመት የተግባር ትምህርት ብቻ እንደሆነ  ታውቋል፡፡ የዚህችን እንስት ጉዳይ ከሌሎቹ ለየት የሚያደርገው በፍ/ቤት መከሰሷ ነው፡፡ በ2012 ዓ.ም ፍ/ቤቱ ጥፋተኛነቷን አረጋግጦ፣ የ14 ወር እስርና የገንዘብ ቅጣት በይኖባታል፡፡ (በኖርዌይ ውሸት ያስከስሳል ማለት ነው?!) እንግዲህ የተለያዩ የውሸት ገፆችና መልኮችን ለመቃኘት ሞክረናል፡፡ የአገራችን የሥነልቦና ባለሙያዎች ዋሾነትን በተመለከተ የሚሰጡት ትንተና ምን እንደሆነ ባላውቅም የውጭዎቹ ግን አደገኛ በሽታ ስለሆነ የህክምና ባለሙያ እርዳታ ያስፈልገዋል ይላሉ። ዋሾዎቹ ወደ ወህኒ ቤት ከመወሰዳቸው በፊትም ሆስፒታል መግባት እንዳለባቸው ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡ እናንተ ምን ትላላችሁ? እንዲህ ከሆነ እኮ ሆስፒታሎቻችን በሙሉ በፖለቲከኞች ሊጨናነቅ ነው፡፡ እነ ዓለም ባንክ የፋይናንስና የባለሙያ እገዛ ካላደረጉልን ነገሩን በራሳችን አቅም ብቻ  እንደማንወጣው እርግጠኛ ነኝ። (ወይስ ፀበል እንሞክር ይሆን?)

አዲሱ የበጀት ዝርዝር ስለ ሠራተኞች ደሞዝ የሚለው ነገር አለ
ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ይኖራል። የግድ ነው። ለምን? ሶስት ምክንያቶች አሉ።
ለመጪው ዓመት የተመደበው የደሞዝ በጀት(ከነመጠባበቂያው)፣ ከዘንድሮው በ66% ይበልጣል
በጀቱና መጠባበቂያው ከ11.5 ቢ ብር ወደ 19.1 ቢ ብር እንዲጨምር ተደርጓል (የ7.6 ቢ ብር ጭማሪ)
ጊዜው የምርጫ ጊዜ ነው። የመንግሥት ሠራተኞችን በከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ማንበሻበሽ ያዋጣል
ግን ማን ያውቃል! የደሞዝ ጭማሪ ላይኖር ይችላል። ለምን? ሶስት ምክንያቶች አሉ
ባልተለመደ ሁኔታ አብዛኛው የበጀት ጭማሪ “መጠባበቂያ” ተብሎ ነው የተያዘው  (6.5 ቢ. ብር)
ጊዜው የምርጫ ነው። ምርጫ ሲቃረብ ደሞዝ እንደማይጨመር አቶ መለስ ዜናዊ ተናግረው ነበር።
የመንግስት ሠራተኞች ወፍራም ጭማሪ ቢያገኙ የዋጋ ንረትና የኑሮ ውድነት ሊፈጠር ይችላል

የመንግስት ሠራተኞችን ደሞዝ በተመለከተ ለ2007 ዓ.ም የተዘጋጀው በጀት፣ ከወትሮው በተለየና ባልተለመደ ሁኔታ፤ የተምታታ ወይም የሚያምታታ ሆኗል። “ደሞዝ ይጨመራል ወይስ አይጨመርም?” ለሚለው ጥያቄ፣ ከበጀት ምደባው ቁርጥ ያለ ምላሽ ማግኘት የለብንም እንዴ? በጀት ማለትኮ እቅድ ነው። በተወሰነ ጊዜ ውስጥ፣ “ይህን ይህን ያህል ገንዘብ ከዚህና ከዚህ አገኛለሁ”፤ “ያንን ያንን ያህል ገንዘብ ለዚያና ለዚያ እከፍላለሁ” ብሎ እቅጩን መናገር አለበት፡፡ የዘንድሮው በጀት ግን፣ በተለይ የሠራተኞችን ደሞዝ በተመለከተ፣ ቁርጡን ለመናገር የፈለገ አይመስልም።
በእርግጥ በ2007 ዓ.ም ለደሞዝ ክፍያ ይውላል ተብሎ የተመደበው አጠቃላይ በጀት፣ በጣም ብዙ ነው። ከዘንድሮው ጋር ሲነፃፀር በ7.6 ቢሊዮን ብር ይበልጣል። ዘንድሮ ለደሞዝ ክፍያ ከነመጠባበቂያው ተይዞ በነበረው 11.5 ቢሊዮን ብር በጀት ላይ፣ ድንገት በአንድ ጊዜ 7.6 ቢሊዮን ብር እንዲጨመርለት የተወሰነው በምን ምክንያት ይሆን? የሠራተኞች ደሞዝ “በወፍራሙ” ካልተጨመረ በቀር ይሄን ሁሉ ገንዘብ መመደብ አስፈላጊ አይደለም። ሌላ ምክንያት ሊኖረው አይችልም። እንዴት በሉ፡፡
የደሞዝ በጀት ላይ ከፍተኛ ጭማሪ የታየበት አመት ቢኖር በ2003 ዓ.ም ነው። ያኔ ታዲያ፤ የደሞዝ በጀት በ40 በመቶ እንዲያድግ የተደረገው፤ በሌላ ምክንያት ሳይሆን ለመንግስት ሠራተኞች የደሞዝ ጭማሪ ስለተሰጠ ነው። የመጪው አመት የደሞዝ በጀት ጭማሪ ግን ከዚህም ይልቃል - ከዘንድሮው በጀት ጋር ሲነፃፀር በ66% ይበልጣል። ይህም ለመንግስት ሠራተኞች ቀላል የማይባል ደሞዝ ለመጨመር መታሰቡን ያረጋግጣል። በዚያ ላይ አስቡት።
የ2007 ምርጫ እየተቃረበ ነው። ገዢው ፓርቲ፣ የደሞዝ ጭማሪውን ለምርጫ ዘመቻ ሊጠቀምበት ከፈለገ፤ ትክክለኛው ጊዜ አሁን ነው።
ደግሞስ ብዙዎቹ የመንግስት ሠራተኞች የገዢው ፓርቲ አባላት አይደሉ? “ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ” በሚለው ፈሊጥ ዳጎስ ያለ የደሞዝ ጭማሪ ቢያሸክማቸው ማንም አይከለክለውም። በእርግጥም ሳያሳንስ የሚቆርሰው ከየራሱ ምጣድና መሶብ እስከሆነ ድረስ፣ “ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ” የሚለው አባባል ቅንጣት ስህተት አይወጣለትም። ችግሩ ምን መሰላችሁ? ለመንግስት ሠራተኞች ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ለመስጠት፣ ገንዘብ ያስፈልጋል። ገንዘቡ ደግሞ ከሰማይ አይዘንብም። ከሌሎች ዜጎች ኪስ መውሰድ የግድ ሊሆን ነው። ከሌሎች ዜጎች ማዕድ ላይ ቆርሶ መውሰድ... ይሄ ነው ችግሩ።
ሌላኛው አማራጭ የብር ኖት በገፍ ማተም ነው። ምን ዋጋ አለው? ይሄኛው አማራጭም፤ የዋጋ ንረትን በማስከተል የዜጐችን ኪስ ያኮሰምናል፡፡
የሆነ ሆኖ፤ ለደሞዝ የሚመደበው በጀት ታይቶ በማይታወቅ ከፍተኛ መጠን እንዲጨምር ተደርጓል። ከምርጫው ጋር ግንኙነት ይኑረውም አይኑረው፤ የገንዘቡ ምንጭ ምንም ይሁን ምን፤ በጀቱ ሙሉ ለሙሉ ሥራ ላይ ሊውል የሚችለው፣ ለመንግስት ሠራተኞች ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ከተደረገ ብቻ ነው። አለበለዚያ የወረቀት በጀት ሆኖ ይቀራል። ስለዚህ የመንግስት ሠራተኞች ያለ ጥርጥር ደሞዝ ይጨመርላቸዋል ብለን በእርግጠኛነት መናገር እንችላለን፡፡
ግን፤ በጀቱ የወረቀት በጀት ሆኖ ቢቀርስ?
እውነት ነው፤ መንግስት ለሠራተኞቹ ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ለመስጠት ቢወስንም፤ ሙሉ ለሙሉ የቆረጠለት አይመስልም። ለምን በሉ። የበጀት ድልድሉ፣ ከሌላው ጊዜ ይለያል። እንደወትሮው ቢሆን፣ አብዛኛው የደሞዝ በጀት፣ ለእያንዳንዱ መሥሪያ ቤት ምን ያህል እንደሚደርሰው በዝርዝር ተሸንሽኖ ይቀርባል። የተወሰነ ገንዘብ ደግሞ መጠባበቂያ ተብሎ ይቀመጣል። ለእያንዳንዱ መሥሪያ ቤት ከተመደበው የደሞዝ በጀት ባሻገር አንዳች ያልተጠበቀና ያልታሰበ ወጪ ቢያጋጥም ችግር አይፈጠርም። የደሞዝ መጠባበቂያ የሚያስፈልገው ለዚህ ለዚህ ነው። ካቻምናና ከዚያ በፊት በየአመቱ 150 ሚ. ብር  የደሞዝ መጠባበቂያ ይመደብ ነበር። አምና ደግሞ 200 ሚ. ብር። ለዘንድሮ የተቀመጠው የደሞዝ መጠባበቂያ 350 ሚ. ብር ነው።
ለመጪው አመት የተመደበው የደሞዝ መጠባበቂያ ግን፣ ከእስከዛሬው በእጅጉ በእጅጉ ይለያል። 6.5 ቢሊዮን ብር ነው የደሞዝ መጠባበቂያ ተብሎ የተመደበው። ለምን? የገንዘብ ሚኒስትሩም ሆኑ የበጀት ሰነዱ፣ በዚህ ጉዳይ ላይ ትንፍሽ ያሉት ነገር የለም። ለነገሩ፤ ጥያቄ ለመሰንዘር ትንፍሽ ያለ ፓርቲ፣ ፖለቲከኛ ወይም ምሁርም የለም። “ለ12.6 ቢሊዮን ብር መደበኛ ደሞዝ 6.5 ቢሊዮን ብር መጠባበቂያ! ኧረ እንዲህ አይነት መጠባበቂያ በታሪክ ታይቶ አይታወቅም! ምንድነው ነገሩ?” የሚል ጥያቄ እስካሁን አልቀረበም።
እንዲህ ጉዳዩ እንደተድበሰበሰ በጀቱ ቢፀድቅ፤ ምን ሊፈጠር እንደሚችል አስቡት። ምንም አይፈጠርም፡፡ መንግስት ለሠራተኞቹ ደሞዝ የመጨመርና ያለመጨመር አማራጮች ይኖሩታል። ከፈለገ ደሞዝ ይጨምራል። የበጀት እጥረት አይገጥመውም። የደሞዝ መጠባበቂያ ተብሎ የተመደበ ብዙ ገንዘብ አለለት። ካልፈለገ ደግሞ ደሞዝ አለመጨመር ይችላል። መጠባበቂያውን ትቶ፤ ለየመሥሪያ ቤቱ ተከፋፍሎ የተመደበውን የደሞዝ በጀት ብቻ ይጠቀማል። በሌላ አነጋገር፣ “መንግስት ደሞዝ ለመጨመርና ላለመጨመር እያመነታ ይሆን ነገሩን በእንጥልጥል ለማቆየት ፈልጐ ይሆን?” ብለን እንድናስብ ይገፋፋናል - ያልተለመደው የበጀት አመዳደብ፡፡
ነገር ግን በደፈናው “የደሞዝ መጠባበቂያ” ተብሎ 6.5 ቢ.ብር የተመደበው በሌላ ምክንያት ሊሆን ይችላል። የበጀት ዝግጅት ሲጀመር፣ ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ መነሳቱ አይቀርም። ከተወሰነ ክርክር በኋላ፣ ሃሳቡ ውድቅ ይሆንና፣ ዝርዝር በጀት ይዘጋጃል። የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ያዘጋጀው ሰነድ እንደሚገልፀው፤ የየመሥሪያ ቤቱ ዝርዝር የበጀት ድልድል የተዘጋጀው የደሞዝ ጭማሪ አይኖርም በሚል መመሪያ ነው፡፡ የበጀት ዝግጅቱ ከተጋመሰ በኋላ ወይም ሊጠናቀቅ ከተቃረበ በኋላ፤ መንግስት ሃሳቡን ቢቀይርስ? ማለትም፤ ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ እንደገና ይነሳል። ለምን?
የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ ስለሚዋዥቅ፤ ከዚሁ ጋር አብሮ የመንግስት ሃሳብም ቢዋዥቅ አይገርምም። ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ ከወራት በፊት ውድቅ ቢደረግ፣ ከጊዜ በኋላ ፖለቲካው ሲንገራገጭ እንደገና ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ ይነሳል፤ ባለቀ ሰዓትም ተቀባይነት ያገኛል። ነገር ግን፣ በዝርዝር የተዘጋጀውን በጀት እንደገና ለመከለስ ቀላሉ ዘዴ ምንድነው? ለደሞዝ ጭማሪ የሚያስፈልገውን በጀት፣ በደፈናው “መጠባበቂያ” ተብሎ እንዲገባ ማድረግ ነው ቀላሉ ዘዴ።
ግን ከምር የሠራተኞች ደሞዝ ይጨመራል? አንዱ ችግር፤ 2007 ዓ.ም የምርጫ አመት መሆኑ ነው፡፡ ታስታውሱ እንደሆነ በ2002 ዓ.ም ለሠራተኞች ደሞዝ እንዲጨመርላቸው ጥያቄ ቀርቦ ነበር፡፡
የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ጥያቄውን አልተቀበሉትም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥያቄውን ውድቅ ያደረጉት “ለመንግስት ሠራተኞች ደሞዝ ሊጨመርላቸው አይገባም” በሚል አይደለም፡፡ ምርጫ በሚቃረብበት ወቅት ለመንግስት ሠራተኞች ደሞዝ መጨመር የአገሪቱን ፖለቲካ እንደሚያበላሽ የተናገሩት አቶ መለስ፤ ኢህአዴግ በምርጫ አመት የደሞዝ ጭማሪ እንደማያደርግ ተናግረው ነበር - በ2002 ዓ.ም፡፡ በ2007ስ?

Page 7 of 18