‘ሰማይ አይታረስ፣ ንጉስ አይከሰስ’ በሚተረትባት፣ ‘እናውቃለን፣ ብንናገር እናልቃለን’ በሚል የሹማምንትን በደል እያወቁ ዝምታን የመረጡ ብዙዎች በሚኖሩባት አገር ከሰሞኑ አዲስ ነገር ተሰማ፡፡ የሚፈሩ ባለስልጣናት፣ ሹማምንትና ባለጠጐች ተከሰሱ፡፡ ይሄን ተከትሎም “…ብንናገር እናልቃለን’ በሚል ስጋት የውስጣቸውን በውስጣቸው ይዘው ሲብሰለሰሉ የኖሩ ብዙዎች ‘ጥቆማ’ ለመስጠት ወደ ስነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን መጉረፍ መጀመራቸውም በየጋዜጣውና በቴሌቪዥኑ ተነገረ፡፡ ስለ ሙስና፣ ስለ ሙሰኞችና ከወትሮው በተለየ ሙስናን ለማጋለጥ መጉረፍ ስለጀመረው “ተበዳይ ህዝብ” ብዙዎች ብዙ ብለዋል፡፡ ብዙዎች ያሉትን ለመድገም አይደለም አነሳሴ፡፡ መንግስት ‘ንጉስም ይከሰሳል’ ብሎ ከማወጁና ሹማምንትን ማሰር ከመጀመሩ፤ ህዝብም አፍኖ የያዘውን የሹማምንት በደል አፍ አውጥቶ በድፍረት ማጋለጥ መናገር ከመጀመሩ በፊት ስለነበረ፣ ስላልተዘገበ፣ ስላልተነገረ ‘አየለ ጀምብ እግር’ የሚባል ሰው ነው የማወጋችሁ፡፡

የሹማምንትንና የባለጠጐችን በደል አፍ አውጥቶ ይተነፍስበት ሁኔታ የተመቻቸለት፣ አቤቱታውን ሰምቶ ፍትህ ይሰጠው አካል የተቋቋመለት፣ ‘የሚያውቀውን’ በመናገሩ አጉል ነገር እንይደርስበት ከለላ የተደረገለት … ይሄ ሁሉ የሆነለት፣ ይሄኛው ትውልድ ስለማያውቀው አየለ እናገራለሁ፡፡ አጭር፣ ወፈር ያለ፣ ፀጉሮቹ የከረደዱ፣ ደማቅ ጠይም ጐልማሳ፤ ሁለቱም እግሮቹ በዝሆኔ ያባበጡ ከሰል ተሸካሚ፡፡ የሚሰማ እንጂ የማይነበብ የሆነ የተለየ ድምጽ ያለው ተረበኛ ሰው ነበር - አየለ። መቼና የት እንደተወለደ ባላውቅም የከሰል ተሸካሚነት ኑሮ ሲገፋ በኖረበት የደብረማርቆስ ጐዳና ላይ ሞቶ እንደተገኘ መረጃ አለኝ፡፡ አየለ ከሞተ ሃያ ያህል አመታት አልፈዋል፡፡ ከእነዚህ አመታት በኋላም ግን የደብረ ማርቆስ ህዝብ አየለን አልረሳውም፡፡ ይሄም ሆኖ ግን ህዝቡ ተሸካሚውን አየለን ዛሬም ድረስ የሚያስታውሰው በጉልበቱ ሳይሆን በአንደበቱ ነው።

እኔም ስለተሸካሚው አየለ ሳይሆን፣ ስለተናጋሪው አየለ ነው የማወጋችሁ፡፡ የህዝቡን ከሰል ሳይሆን የህዝቡን በደል በትክሻው ይዞ ሲመላለስና ወደተፈለገው ቦታ ሲያደርስ ስለኖረው “ተናጋሪው አየለ” ነው የማጫውታችሁ። አየለ ማን ነበረ? እሱ በደል አንገብግቦት ውስጥ አንጀቱ ያረረ፣ ‘አቤት’ ይልበት ወኔም አንደበትም ያልነበረው የደ/ማርቆስ ህዝብ ‘አፍ’ ነበረ፡፡ የሹማምንትንና የባለጠጐችን ግፍ በየጓዳው ውስጥ ውስጡን ማጉተምተም እንጂ፣ ‘አቤት’ ብሎ አደባባይ ሊወጣ ያልደፈረን ተበዳይ ህዝብ መራራ ሀቅ፣ በበዳይ ሹማምንት ፊት ቆሞ በድፍረት ሲናገር የኖረ የአገር ‘አንደበት’ ነበረ፡፡ በቀልድ እየቀመመ፣ በፌዝ እያስታመመ፣ በስላቅ እያከመ በሚተነፍሰው የታፈነ የህዝቡ መራራ እውነት የሚታወቅ፣ የህዝብ ሃቅ፣ የህዝብ ሳቅ ነበረ አየለ፡፡ የከንቲባው ቦርሳ በደርግ መንግስት የመጨረሻዎቹ አመታት የደብረ ማርቆስ ከተማ ከንቲባ የነበሩት ‘ጓድ እንትና’፣ እጅግ የሚፈሩና የሚከበሩ ባለስልጣን ነበሩ፡፡

ግርማ ሞገሳቸው ከሩቅ የሚያስፈራው ‘ጓድ እንትና’ የከተማዋን መሪ በሁለት እጆቻቸው ጨብጠው፣ ህዝቡን ባሻቸው አቅጣጫ የመምራት ፍፁም ስልጣን ነበራቸው ይባላል፡፡ ይሄም ብቻ አይደለም። በየጐዳ ጐድጓዳው ስለ ከንቲባው የሚወራውና የሚባለው ነገር ብዙ ነው፡፡ ህዝቡን ያለ አግባብ ስለመበደላቸው፣ ስለ ጉቦኛነታቸው፣ የህዝቡን ገንዘብ ያለ አግባብ በግል ካዝናቸው ስለማጨቃቸው … ብዙ ብዙ ነገር ይወራባቸዋል፡፡ ይሄም ሆኖ ግን ወሬውም ሃሜቱም ውስጥ ውስጡን ነው፡፡ እኒህ የታፈሩና የተፈሩ ከንቲባ ‘እንዲህ አደረጉ’ ብሎ አፍ አውጥቶ መናገር፣ በገዛ እጅ በራስ ላይ መከራ መጥራት በሆነባት፣ አዋሻኪና አሳባቂ ጆሮ ጠቢ በሞላባት ከተማ፣ የልቡን ለመናገር የደፈረ አየለ ብቻ ነበረ፡፡ የአየለን ድፍረት የተለየ የሚያደርገው፣ በአደባባይ ስለ ከንቲባው አጉል ነገር መናገሩ ሳይሆን፣ ይሄን አጉል ነገር ለራሳቸው ለከንቲባው መናገሩ ነው፡፡ አንድ ዕለት ‘ጓድ እንትና’ ስራ ውለው ወደ ቤታቸው ሲመለሱ፣ ከአየለ ጋር መንገድ ላይ ይገጣጠማሉ፡፡ ከንቲባው በእጃቸው ሳምሶናይት ቦርሳ ይዘው እንዳላዩ ሊያልፉት ሲሉ ታዲያ፣ አየለ ሆዬ ቆም ብሎ በፈገግታ ይመለከታቸዋል፡፡ “ደህና ዋሉ ጓድ እንትና?” በማለትም ሰላምታ ይሰጣቸዋል፡፡

“ሰላም ነህ?” ብለውት ጉዟቸውን ሊቀጥሉ ይዘጋጃሉ፡፡ አየለ ከንቲባው ወደያዙት ቦርሳ እያየ በትሁት አንደበት መናገሩን ቀጠለ፡፡ “እሷን ነገር ላግዝዎት ይሆን?” “አይ! … ደርሻለሁ … አመሰግናለሁ” ከንቲባው ነገሩን በአጭር ቋጭተው ከዚህ ነገረኛ ሰው ለመምለጥ ፈልገዋል፡፡ እሱ ታዲያ መች በዋዛ የሚለቃቸው ሆነ “ኧረ ግዴለም ትንሽ እንኳን ልርዳዎት?... የህዝብ ገንዘብ እኮ ይከብዳል” ብሏቸው እርፍ፡፡ ከንቲባው ምንም አላሉም፡፡ ለነገሩ ምንስ ማለት ይችላሉ? ሽሙጥ በሽጉጥ አይመለስ! ‘ጓድ እንትና’ ሰምተው እንዳልሰሙ ወደ ቤታቸው ቢገቡም፣ ወሬው ግን ሳይውል ሳያድር በየመንደሩ ተሰማ፡፡

አየለ እንዲህ እንደ ከንቲባው የማይደፈሩ የከተማዋ ጉቦኛ ሹማምንትና “ኪራይ ሰብሳቢ” ባለጠጐችን በሽሙጥና በነገር ወጋ ማድረግ ልማዱ ነው፡፡ በአብዛኛው በሽሙጥ እና በስላቅ ዘወርወር አድርጐ የልቡን የመናገር ልማድ የነበረው አየለ፣ አንዳንዴ ግን በየጓዳ ጐድጓዳው የተደበቀውን ሐሜት በአደባባይ ፍርጥርጥ አድርጐ ለመናገርም አያመነታም፡፡ እርግጥ እንዲህም ሆኖ ደረቅ ዘለፋ ብሎ ነገር አይነካካውም፡፡ “ሰርቋል”፣ “በድሏል”፣ “ዘሙቷል”፣ “አታላለች” አይልም አየለ፡፡ ባለ ሆቴሉ ጋሽ እንትና፣ ሆቴሉን ከመክፈታቸው ከጥቂት አመታት በፊት ከእጅ ወደ አፍ ኑሮ የሚገፉ የትምህርት ቢሮ ተቀጣሪ ተራ የመንግስት ሰራተኛ ነበሩ፡፡ ድንገት የመንግስት ስራቸውን በገዛ ፈቃዳቸው ለቀው ባለሁለት ፎቅ ህንፃ የገነቡትንና የሚያምር ሆቴል የከፈቱትን ጋሽ እንትናን ህዝቡ ክፉኛ ያማቸዋል፡፡ አንድ ምሽት አየለ ወደ ሆቴሉ ገብቶ ለመዝናናት ሲሞክር፣ ጋሽ እንትና በዘበኛ ያሳግዱታል፡፡ “ይተውኝ እንጂ ጋሽ እንትና? ምናለበት እኔስ እንደሌላው ሰው ከፍዬ ብበላ ብጠጣ?” በማለት በትህትና ጠየቀ አየለ፡፡ “አይሆንም…ከዛሬ ጀምሮ እዚህ ሆቴል አትገባም ብያለሁ አትገባም!” ፈርጠም አሉ ጋሽ እንትና፡፡ “ምን ባጠፋሁ ጋሽዬ?” መልሶ ጠየቀ፡፡ “እየተሳደብክ አስቸግረሃል…ባንተ ምክንያት ደንበኞቼ እንዲርቁኝ አልፈልግም …ከአሁን በኋላ ሆቴሌ ውስጥ እየገባህ እንደፈለግህ መዘባረቅ አትችልም” ጋሽ እንትና ማምረራቸውን ገለፁ፡፡

አየለም የበለጠ ይምረራቸው ብሎ ቀጠለ፡፡ “እስቲ ይንገሩኝ ጋሽዬ…ምን ብዬ ዘባረቅኩ?...”የትምህርት ቢሮን ገንዘብ ዘርፈው ፎቅ ሰሩ” አልኩ? እንደማንም ሃሜተኛ “ከመንግስት በዘረፉት ብር ሆቴል ከፈቱ” ብዬ ተናገርኩ?...እስቲ ይንገሩኝ ምን ብዬ ዘባረቅኩ?” አለ፡፡ ከጋሽ እንትና አንደበት ቀድሞ መልስ የሰጠው የዘበኛው ዱላ ነበር፡፡ የደብረ ማርቆስ ህዝብ በአጉል ነገር ውስጥ ውስጡን የሚያማቸው እንደ ጋሼ እንትና ያሉ ባለጠጐች፣ የአየለን ምላስ እንደ ጦር ይፈሩታል፡፡ የሚያሳማ ጉዳይ ያለባቸው ሁሉ ‘እንዳያዋርደን’ በሚል ስጋት በቻሉት መንገድ ሁሉ አየለን ላለማስቀየምና ወዳጅ ለማድረግ ይጥራሉ፡፡ “አየለ … ና … እንጂ ሻይ ጠጣ” “እስቲ በቁምህ አንድ ሁለት ብለህ ሂድ” “እንካ እስኪ ይቺን … ባይሆን ለጠላ ትሆንሃለች” እንዲህና እንዲያ ባዩ ብዙ ነው፡፡

አንድ ዕለት ታዲያ… ጓደኛሞች የሆኑ ሰዎች አንድ ሆቴል በረንዳ ላይ ሰብሰብ ብለው ሻይ ቡና እያሉ ሲጨዋወቱ አየለን አልፎ ሲሄድ በቅርብ ርቀት ያዩታል፡፡ ከመካከላቸው አንዱ (የሚያሳማ ነገር ያለበት ሳይሆን አይቀርም) ጮክ ብሎ ወደ አየለ እያየ ይጣራል፡፡ “አየለ … ሰማህ ወይ አየለ?” “አቤት” አየለ ቆም ብሎ ወደ ሰዎቹ እያየ መልስ ሰጠ፡፡ “ና እንጂ የሆነ ነገር ብለህ ሂድ?” አለ ሰውዬው፡፡ ልጋብዝህ ማለቱ ነው፡፡ “አይ! … የለም ይቅርብኝ!” አለ አየለ - ትክሻውን በእምቢታ እየነቀነቀ፡፡ “አንተ ደ’ሞ … ሰው ሲለምንህ’ማ እሺ በል” አለ ሌላኛው፣ ‘አልጋበዝከኝም’ ተብሎ እንዳይታማ የፈራ ሰውዬ ወደ አየለ እያየ በልመና፡፡ “ኧረ እኔ እቴ!... የለም…ተውኝ ልሂድ!” ድርቅ አለ አየለ፡፡ “ምናለበት ገባ ብለህ አንድ ሁለት ብትል?...” ቀጠለ ሌላኛው “የለም … አልገባም!... እህል ቀምሻለሁ!” አለ አየለ ሆቴሉን የጐሪጥ እያየ፡፡ የሆቴሉ ባለቤት “ታቦትና የቤተ ክርስቲያን ንዋየ ቅዱሳት” ዘርፈው በመሸጥ በህገ ወጥ መንገድ ሃብት ያፈሩ ናቸው’ በሚል በከተማዋ ህዝብ ክፉኛ የሚታሙ ናቸው (እህል ተቀምሶ ቤተክርስቲያን ውስጥ እንደማይገባ ልብ ይሏል)፡፡ በታቦት ገንዘብ የተሰራ ሆቴል፣ ‘ቤተክርስቲያን ነው’ ማለቱ ነው አየለ፡፡


“ወያኔ” እንደገባ “አየለ ጀምብ እግር” በሽሙጥ ጐንተል ከሚያደርጋቸው ሰዎች ከግልምጫ እስከ ጡጫ የሚደርስ ምላሽ ይሰነዘርበታል፡፡ እሱ ግን ይሄን ሁሉ መአት የሚመክትበትና ከጥቃት የሚያመልጥበት መላው፣ አሁንም ምላሱ ነው፡፡ ኢህአዴግ ደብረ ማርቆስን የተቆጣጠረ ሰሞን እንዲህ ሆነ፡፡ አንድ ምሽት … አየለ ጠላ ቤት ውስጥ ቁጭ ብሎ እየቀመቀመ እያለ ከአንድ ወጣት ጋር ይጋጫል፡፡ ወጣቱ አየለን ለመደባደብ እየተገለገለ ‘ያዙኝ ልቀቁኝ’ ይላል፡፡ አየለ ግን ጠላውን እየደጋገመ ‘ኧረ እዲያ እቴ…’ እያለ በዚያች ደም የምታፈላ አብሻቂ ቅላፄው በጠበኛው ላይ ያሾፋል፡፡ የወጣቱ ፉከራም እያየለ ይመጣል፡፡ “አንተ ግንድ እግር! ገላጋይ አለ ብለህ ነው አይደል የምትቀባጥረው? … ወንድ ከሆንክ ውጭ እንወጣና ይለይልን” እያለ በንዴት ይንቀጠቀጣል - ወጣቱ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያለ ጠጪው ሒሳቡን ከፍሎ ወደእየቤቱ ይሄዳል፡፡ ገላጋይ ይጠፋል፡፡ ወጣቱም ከጠላ ቤቱ በመውጣት ደጃፍ ላይ ቆሞ አየለን አፈር ድሜ ለማስገባት ይጠባበቃል፡፡ ባለ ጠላ ቤቷ ቤታቸውን ለመዝጋት ሲዘጋጁ፣ መቼም ባመሸበት አያድርምና በስተመጨረሻ አየለም ከጠላ ቤቱ ይወጣል፡፡ ወጣቱ ከጠላ ቤቱ በር ራቅ ብሎ ቆሞ ለድብድብ ሲዘጋጅ ያየዋል፡፡ አለፍ ብሎ ደግሞ ታጣፊ ክላሽ ያነገቱ “ወያኔዎች” ሮንድ እየጠበቁ ይመለከታል፡፡ ወጣቱ በንዴት እየጮኸ መዳፎቹን ለቦክስ አዘጋጅቶ ወደ አየለ ሲጠጋ ያዩት ሮንዶች፣ ክላሻቸውን አንቀጫቀጩና ወደ እነ አየለ ተንደረደሩ፡፡ “ቁም እንዳትንቀሳቀስ!...የምን ጭቅጭቅ ነው?” ጠየቀ አንደኛው ባለ ክላሽ፡፡ አየለ ወደ ወጣቱ እየጠቆመ ፈጣን ምላሽ ሰጠ፡፡ “ኧረ እኔ እንጃ እቴ!... ዝም ብሎ ይጨቀጭቀኛል!... እኔስ እሚለውም አልገባኝ፣ እስቲ እንግዲህ እናንተ ጠይቁት! … ‘መንጌ፣ አንተ ትሻለናለህ” ይላል!... ‘የማንም ጨብራራ መጫወቻ ሆነን ቀረን’ ይላል! …‘በአህያ ነው የመጡት’ ይላል … እነማንን እንደሆን እንጃ … እስቲ ጠይቁት” እያለ ቀጠለ አየለ፡፡ “እደባደባለሁ” እያለ ሲገለገል የነበረው ወጣት በክላሽ ሰደፍ እየተደቃ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ተወሰደ፡፡ አየለም ወደ ቤቱ!


“አየለ ጀምብ እግር” በነገር ወጋ እያደረገ ያስቀየማቸው አንዳንዶች፣ “አፉ ባለጌ ነው” ይሉታል፡፡ እርግጥ አየለ ተሳዳቢ ነው ሊባል ይችላል፡፡ ይሄም ሆኖ ግን “ተሳደበ” ቢባል እንኳን ልብ የሚያቆስል ሽሙጥ እንጂ፣ የብልግና ቃል እምብዛም ከአፉ ሲወጣ አይደመጥም፡፡ ይልቁንም ህፃን አዋቂው ወደ አየለ የሚወረውረው የብልግና ቃል ይበልጣል፡፡ የጤና ችግሩ መጠሪያው ሆኖ “አየለ ጀምብ እግር” ሲባል ምን እንደሚሰማው መገመት አያዳግትም፡፡ አንድ ወጣት ነው አሉ፡፡ ከሰል ተሸክሞ የሚጓዘውን አየለን ከበስተኋላው እየተከተለ በግጥም ይወርፈዋል፡፡ “ፍየል በግርግር አየለ ጀምብ እግር” እያለ፡፡ አየለ መልስ ሳይሰጥ ጉዞውን ቀጠለ፡፡ ወጣቱ ግን አሁንም መሳደቡን አላቆመም፡፡ “አየለ ወሸላ (ይቅርታ)” ይለዋል ጮክ ብሎ፡፡ ስድቡ ከተሸከመው ከሰል በላይ የከበደው አየለ፣ ተሳዳቢውን ወጣት ዞር ብሎ በንቀት እየተመለከተ የመልስ ምት ለመስጠት ተዘጋጀ፡፡ “አየለ ወሸላ!” ደገመ ወጣቱ፡፡ “አይ!...የሰው ነገር!...ያቺ እናትህ ይሄንንም ሚስጥር ብላ ነገረችህ?!” አለ አየለ፡፡ እንዲህ ነው አየለ፡፡ እንዲህ ያለውን አይን ያወጣ ዘለፋ በሰምለበስ ምላሽ ነው የሚመክተው፡፡


ምንም እንኳን ቀደም ብዬ እንደገለፅኩት አየለ የሚተዳደረው በሸክም ቢሆንም፣ ከሌሎች ተሸካሚዎች በተለየ እንዲታወቅና ተፈላጊ እንዲሆን ያደረገው ጠንካራ ጉልበቱ ሳይሆን ጠንካራ አንደበቱ ነበር፡፡ በስላቅ እንዳይዳብሳቸው ሰግተው የሚሸሹት የመኖራቸውን ያህል፣ በሳቅ እንዲያፈርሳቸው ሽተው በየሄደበት የሚከተሉት ብዙ ነበሩ፡፡ የአየለን ንግግር ለመስማት የሚጓጉና ዱካውን ተከትለው የሚያፈላልጉት ብዙዎች ነበሩ፡፡ ‘አየለ አለበት’ የተባለ ጠላ ቤት፣ ከአፍ እስከ ገደፉ ነበር የሚሞላው፡፡ ይህን ስለሚያውቁ ነው ጠላ ጠማቂ ሴቶች አየለን ሳይነጋ የሚያፈላልጉትና እንጀራ በአዋዜ ቁርሱን አብልተው ዘመራ ጠላ ሲያስኮመኩሙት የሚውሉት፡፡ ታዲያ በነፃ ነው፡፡ ሲጠጣ ውሎ ሲጠጣ ቢያድር ‘ሒሳብ’ ብሎ የሚጠይቀው የለም፡፡ ለእሱ የሚቀዳው የነፃ ጠላ፣ እሱን ተከትሎ ሳቅ ፍለጋ ወደ ጠላ ቤቱ ለሚጐርፈው ጠጪ የተከፈለ የማስታወቂያ ወጪ ነው፡፡ በጠላ ጠማቂዋ ስፖንሰርነት በነፃ ሲጠጣ ስለሚውል ከጠጪዎች የሚያገኘው ግብዣ በቀጥታ ወደ ኪሱ የሚገባ የዕለት ገቢው ይሆናል፡፡ በዝሆኔ በሽታ የተጠቁ ሁለት እግሮቹ፣ ችግሮቹ ሳይሆን መጠሪያዎቹ ሆነው ልጅ አዋቂው “አየለ ጀምብ እግር” እያለ ነው የሚጠራው፡፡

አየለ ግን በእግሮቹ ሲሳለቅ እንጂ ሲሳቀቅ አይታይም። ሲጠጣ ውሎ ወደ ቤቱ እየተጓዘ ነው፡፡ ሚዛኑን ስቶ መንገዳገድና እግሮቹም እርስበርስ መጋጨት ጀምረዋል፡፡ አየለ እንደምንም ቆም ብሎ እግሮቹን እያየ በግርምት ተናገረ፡፡ “እኔ'ኮ የሚገርመኝ…ምን ሆንን ብላችሁ ነው የምትጋጩት?...የማበላችሁ እኔ!...የማጠጣችሁ እኔ!...ምናለ ተስማምታችሁ ብትኖሩ?!” በማለት፡፡ ከትላልቅ እግሮቹ ጋር በተያያዘ የነበረውን ሌላ ገጠመኝ ላክልላችሁ፡፡ አንድ ምሽት ጨለማን ተገን አድርጐ ወደ ሴተኛ አዳሪ ጐራ ይላል አሉ፡፡ መብራት ስላልነበር ሴተኛ አዳሪዋና አየለ ጨለማ ውስጥ ነበር ስለ ጉዳዩ ተነጋግረው የተስማሙት፡፡ ድርድሩ ተጠናቅቆ አየለ ቀደም ብሎ አልጋው ውስጥ ገብቶ ሴተኛ አዳሪዋን መጠበቅ ጀመረ፡፡ ጥቂት ቆይቶ እሷም ጣጣዋን ጨርሳ መጣችና ብርድልብሱን ከፍታ ከጐኑ ተኛች፡፡ ነገሩ ከመጀመሩ በፊት ግን፣ ሴተኛ አዳሪዋ ከግርጌዋ የሆነ ከበድ ያለ ነገር ሲጫናት ተሰማት፡፡ ደንገጥ ብላም አማተበች፡፡ “ኧረ የምን ጉድ ነው፣ አልጋው ስር የተጋደመው አንቱዬ?” አለች ሴተኛ አዳሪዋ በእግሮቿ የከበዳትን ነገር ለመሸሽ እግሮቿን እያጣጠፈች፡፡ ነገሩ የገባው አየለ ፈጥኖ መለሰላት፡፡ “አይዞሽ አትደንግጭ!...ጫማዬን ሳላወልቅ ተኝቼ ነው!” ወደማደሪያው ያቀናል - ደ'ሞ በራሱ እየቀለደ፡፡


ኢህአዴግ ደ/ማርቆስ መግባቱን ተከትሎ … ከዚህ በፊት የጠቀስኳቸውና አየለ በነገር ወጋ ያደረጋቸው የደርግ ባለስልጣን (የደ/ማርቆስ ከንቲባ) እንደሌሎች ኢሰፓዎች ሁሉ ተይዘው ወደ እስር ቤት ገቡ፡፡ ኢህአዴግ ከንቲባውን ያሰራቸው በስልጣን ዘመናቸው በሰሩት ግፍ ሊሆን እንደሚችል መገመት አያዳግትም፡፡ አየለን ያሰረበትን ምክንያት ግን የሚያውቅ ያለ አይመስለኝም፡፡ የሆነው ሆኖ በአንድ ወቅት ከንቲባውና አየለ እስር ቤት ተገናኙ፡፡ አንድ ዕለት ታዲያ እስረኞች በተወሰነ ሰአት በሰልፍ ወደ መፀዳጃ ቤት ሲወሰዱ አየለና ከንቲባው በአጋጣሚ ጐን ለጐን ይቀመጣሉ፡፡ አየለ ከከንቲባው ጐን ቁጭ ብሎ እየተፀዳዳ በዚያች አሽሟጣጭ ቅላፄው እንዲህ አለ፡፡ “ወይ ጉድ እናንተዬ!...ወያኔ እመጣ ብሎ፣ እኔና ጋሼ እንተናም አብረን ያልበላነውን አብረን እናስወጣው ጀመር?!”


የቀልድ ህይወት ፣ የምር ሞት! ተረበኛው፣ ቀልደኛው፣ ዋዘኛው፣ ፌዘኛው አየለ በ1980ዎቹ መጨረሻ አንድ ማለዳ ከመንገድ ዳር ሞቶ ተገኘ፡፡ ሲጠጣ አምሽቶ በስካር ናውዞ ወደ ማደሪያው በመጓዝ ላይ እያለ የጣለው ሃይለኛ ዝናብ ክፉኛ ደብድቦት፣ ቱቦ ስር ወድቆ በላዩ ላይ ጐርፍ ሲሄድበት አድሮ ጧት ላይ አስከሬኑ ደለል ሰርቶ ታየ።

የአየለ ሞት በመላ ደብረ ማርቆስ ተሰማ። ይሄን ተከትሎ በከተማዋ የሚታወቁ በርካታ ባለሃብቶች በተለያዩ ጊዜያት ከአየለ የተቀበሉትን አደራ ይዘው ወጡ፡፡ “እኔ ጋ 2 ሺህ ብር አለው” “ይሄው…1ሺህ 200 ብር” “ሶስት መቶ ብሩ ይሄውላችሁ” የሚለው የባለሃብቶች ያልተጠበቀ ንግግር ተደመጠ፡፡ አየለ በኑሮው እንጂ በሞቱ ቀልድ እንደማያውቅ የታወቀው በዚህ ጊዜ ነው፡፡ በህይወት እያለ ስለ ቀብሩ እንጂ ስለ ኑሮው አይጨነቅም ነበር። በጉልበቱም በአንደበቱም የሚያገኘውን ገንዘብ እያጠራቀመ፣ ለባለሃብቶች በአደራ ይሰጥ ነበር፡፡ “መቼም መሞቴ አይቀርም… ማስቸገር አልፈልግም። እኔን ለመቅበርም የከተማው ህዝብ መጉላላት የለበትም፡፡ ባይሆን ለቀብሬ እንኳን ራሴን ልቻል እስኪ እቺን ብር አስቀምጡልኝማ” ከሚል ቀልድ የሚመስል የምር አደራ ጋር፡፡ አየለ እንደተመኘውም “ራሱን ችሎ” ተቀበረ፡፡ የደብረ ማርቆስ ህዝብ አስከሬኑን ወደ መቃብሩ የሸኘው በመንታ እንባ ነው፡፡ ለቀልደኛ ህይወት እና ለምር ሞት!

Published in ህብረተሰብ
  • ጋዜጠኝነትን ለማበረታታት የተዘጋጀ ውድድር ነው---
  • የራሳችንን ታሪክ ራሳችን ወደ መናገር ማደግ አለብን----
  • ልጄ ደውሎ እንዴት ነች ኢትዮጵያ ብሎኛል-----

አፍሪካን ሚዲያ ኢኒሽየቲቭ (አሚኢ) በልማት መስክ ለሚሠሩ ጋዜጠኞች “አፍሪካን ስቶሪ ቻሌንጅ” የተሰኘ ውድድር በማዘጋጀት ለአሸናፊዎች ሽልማት እንደሚሰጥ ባለፈው እሁድ በአዲሱ ካፒታል ሆቴል የማስተዋወቂያ ዝግጅት ላይ አስታውቋል፡፡ ካለፈው እሁድ ጀምሮ የጋዜጠኞችን የመወዳደርያ ፕሮፖዛል መቀበል የጀመረው አሚአ፤ እስከ ሰኔ 7 ድረስ ፕሮፖዛል እንደሚቀበል ገልጿል፡፡ የመጀመሪያ ዙር ውድድሩ በግብርና ዙሪያ እንደሆነ የታወቀ ሲሆን ውድድሩ ለአፍሪካውያን ጋዜጠኞች ብቻ የተዘጋጀ ነው ተብሏል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ መልካሙ ተክሌ የቀድሞው የቢቢሲ አፍሪካ አገልግሎት ዋና አዘጋጅና የአሚኢ አርታዒ ከሆነው ኬንያዊ ጋዜጠኛ ጆሴፍ ዋሩንጉ ጋር በውድድሩ፣ በሙያውና በግል ሕይወቱ ዙርያ ቃለምልልስ አድርጎለታል፡፡

የውድድሩን ሃሳብ ያመነጨው ማነው? ሀሳቡን ያመነጨው አፍሪካ ሚዲያ ኢንሽየቲቭ ነው፡፡ የአፍሪካ መገናኛ ብዙሃን ጠንካራና ነፃ እንዲሆኑ ይፈልጋሉ፡፡ ስለዚህም ከመገናኛ ብዙሃን ባለቤቶች ጋር ይሰራሉ፡፡ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ይከታተላሉ፡፡ ድርጅቱ ከሁሉም የአፍሪካ መገናኛ ብዙሃን ጋር ግንኙነት አለው። ለሬዲዮም ሆነ ለጋዜጣ የሚሆን ሃሳብ ኖሯቸው በአቅም ማነስ መስራት ያልቻሉትን ለማገዝ የታለመ ነው፡፡ ውድድሩ በልማት ታሪኮች ላይ ያተኩራል፡፡ ሽልማቱ በሞ ኢብራሂም፣ በቢልና ሜሊንዳ ጌትስ ፋውንዴሽን እና በሌሎችም የሚደገፍ ነው፡፡ ድጋፍ አድራጊዎች በጋዜጠኛው ጽሑፍ ምዘና ላይ ተጽዕኖ አያሳድሩም? እውነት ነው፡፡ እንቀበለዋለን፡፡ ድጋፍ አድራጊዎቹ የኢዲቶሪያል ነፃነቱን የጠበቀ የጋዜጣ ጽሑፍ ወይም የሬዲዮ ዝግጅት መኖር እንዳለበት ያውቃሉ፡፡ እኔ የውድድሩ የ”አፍሪካን ስቶሪ ቻሌንጅ” አርታዒ ነኝ፡፡

እኔ ነኝ የምወስነው እንጂ ፈንድ አድራጊዎቹ አይደሉም፡፡ ገለልተኛ የዳኞች ቡድንም አለን። እስካሁን ስምንት ናቸው፡፡ ለወደፊት የዳኞቹን ቁጥር 20 ለማድረስ አቅደናል። እነሱ ናቸው ውጤት የሚያሳዩት፡፡ የኛ ሥራ የተወዳዳሪዎችን የተጣራ ዝርዝር ማዘጋጀት ነው፡፡ እነዚህን ፈንድ አድራጊዎች የፈለግነው አፍሪካን ሚዲያ ኢኒሽየቲቭ ልማት ላይ መሥራት ስለሚፈልግ ነው፡፡ የቢል እና ሚሊንዳ ጌትስ ፋውንዴሽን፣ እንዲሁም የሞ ኢብራሂም ፋውንዴሽን በልማት ላይ ነው የሚሰሩት፡፡ ይኼ ሁሉ ሆኖ በመጨረሻ ይዘቱን የሚወስነው ግን ጋዜጠኛው ነው፡፡ ለውድድሩ ከቀረቡት ጽሑፎቹ መካከል ድጋፍ ሰጪዎቹን የሚሸነቁጡ ቢኖሩስ? ይሄ የጋዜጠኞቹ ጉዳይ ነው፡፡ በይዘት ጣልቃ አንገባም፡፡ እኛ የጋዜጠኝነትን መርሕ ተከትሎ መዘጋጀቱን እና ተዛማጅ ጉዳዮችን ነው የምናየው። የጋዜጠኞች የግንኙነት መረብ እንዲጠናከር እንፈልጋለን፡፡

አፍሪካ ውስጥ በጋዜጠኝነት መሥራት ከባድ ነው ይባላል፤ ሽልማቱ የአንድ ወገን ጥገኛ የመሆን አዝማሚያ አያሰጋውም? ቅድሚያ የምንሰጠው ለፕሮፌሽናሊዝም ነው። የምንፈልጋቸው ጽሑፎችም ሆኑ የምንሰጣቸው ድጋፎች በዚህ መሠረት ነው፡፡ ይኼንን ወይንም ያንን ደግፍ ንቀፍ የሚባልበት አይደለም፡፡ ጋዜጠኛው ስለ ሰዎች አንድ ታሪክ ስለፃፈ “ፀረ መንግስት ነው”፣ “መንግስት ደጋፊ ነው” መባል የለበትም፡፡ ስለነጋዴዎች፣ ሐኪሞች፣ ገበሬዎች ነው የሚፃፈው፡፡ ትክክለኛ ያልሆነ ፖሊሲ ነው፣ እርሻን አያዳብርም፣ ንግድ አያስፋፋም ማለት ይቻላል፤ የሙያ ሥነምግባሩን ጠብቆ፡፡ ሰዎች ካንዱ ሌላውን ያምናሉ ካልክ እስማማለሁ፡፡ የሚታተሙት ታሪኮች ከአፍሪካ አልፈው በአሜሪካና በሌሎችም አለማት እንዲነበቡ እንፈልጋለን፡፡

ውድድሩ ለምን በእርሻ ላይ ብቻ ሆነ? ለምሳሌ ለምን በዲሞክራሲ ሥርዓት ላይ አልሆነም? የለም…የለም እርሻ ላይ ብቻ አይደለም፡፡ የእርሻ ልማት የመጀመሪያ ዙር ውድድር ነው፡፡ አምስት ዙሮች አሉ፡፡ ጤና፣ ቢዝነስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ኢኖቬሽን እና “አፍሪካዬ በ2063” በሚሉ ርእሰ ጉዳዮችም ውድድር ይካሄዳል፡፡ በማንኛውም የመገናኛ ብዙሃን ተቋም በቂ የፖለቲካ ዘገባ ሽፋን አለ፡፡ በጤና እና ግብርና ጉዳዮች ይሄን አታገኝም፡፡ ይኼን ነው ለማመጣጠን እየጣርን ያለነው፡፡ ለሽያጭ በሚቀርቡ ጋዜጦች ላይ ግብርናን ርእሰ ጉዳይ ማድረግ አያስቸግርም? አርታኢዎች ጋዜጣ መሸጥ አለባቸው፡፡ የሚፃፉት ታሪኮች መነበብ አለባቸው፡፡ በዚህ ውድድር እንዴት ተነባቢ የግብርና ጽሑፎች ማዘጋጀት ይቻላል በሚለው ላይ እንሰራለን፡፡ አንባቢዎች ሌሎች ጽሑፎች መርጠው እንደሚያነቡት ሁሉ ጥሩ ሆኖ ከተፃፈ አሪፍ የእርሻ ጽሑፍ አነበብኩ ይላሉ፡፡ ከውድድሩ በፊት ሥልጠና እንሰጣለን፡፡

አርታዒው ጥሩ ተደርጐ ተጽፏል ብሎ አትመዋለሁ የሚለውና አንባቢውም ተሻምቶ የሚያነበውን ጋዜጠኛው መፃፍ አለበት፡፡ አንባቢ ወድጄዋለሁ ካላለ ፅሁፉ ተነባቢ አይደለም ማለት ነው፡፡ እንደ አንጋፋ ጋዜጠኛነትህ ጥሩና ሳቢ ጽሑፍን እንዴት መፃፍ ይቻላል? ቁጥር አንድ ሕዝብ ነው፡፡ ስለ ሕዝብ መፃፍ አለበት፡፡ ፅሁፉ በሰው ላይ ተጽእኖ ሊያሳድር ይገባል፡፡ ሳነበው የገበሬውን ስቃይ እንዲሰማኝ ሆኖ መፃፍ አለበት፡፡ ሲደሰትም ደስታውን መጋራት እችላለሁ፤ ጥሩ ተደርጐ ከተፃፈ፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ከጥሩ ምንጭ መረጃ መጠናቀር አለበት፡፡ ትክክለኛ መሆን እና አሀዞቹም መረጋገጥ አለባቸው፡፡ ቋንቋና ስልቱም ለመነበብ ቀላል መሆን እና ከሙያ ቃላት በተቻለ መጠን የራቀ መሆን አለበት፡፡ ስለ ጤና ስታወራ እንደ ዶክተር መናገር የለብህም፡፡ ታንዛንያ ላይ የፃፍከው ጽሑፍ እዚህ ኢትዮጵያ መጥቶ ከእኔ ጋር ምን ግንኙነት አለው፣ ብለህ ልታነበው ይገባል፤ ደህና አድርገህ ከፃፍከው፡፡ የሚያገናኝ ነገር ሊኖረው የግድ ይላል፡፡ ኢትዮጵያ ለራሷ ታግላ መፍትሔ ያገኘችለት የግብርና ርእሰ ጉዳይ በሌላ ሀገርም ፍላጐት ያጭራል፡፡ ዋናው ነገር ታሪኩ ሰው ሰው መሽተቱና ስሜት መንካቱ ነው፡፡ ግን እኮ አንዱ ጥሩ ታሪክ ነው ያለውን ሌላው መጥፎ ነው ሊለው ይችላል… እውነት ነው፡፡

ታሪኩ በተቻለ መጠን የብዙ ሰዎችን ቀልብ የሚገዛ ሊሆን ግን ይችላል። ውስን ከሆነ ግን አንባቢው አይመለከተኝም ብሎ ላያነብ ይችላል፡፡ በአንባቢው ላይ ተጽእኖ የሚያሳድርና መንግስት ያወጣውን ፖሊሲ እስከ ማሻሻል የሚያደርስ ሊሆን ይችላል፡፡ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን የሚዳስስም ሊሆን ይችላል። በኢትዮጵያ የመሬት ወረራ አለ ብዬ አስባለሁ፡፡ በኬንያና በሌሎችም ሀገራት አነጋጋሪ ርእሰ ጉዳይ ነው፡፡ ለኢንቨስተሮች መሬት ለመስጠት ሰዎች ሲፈናቀሉ ምን ይሆናሉ፡፡ እነዚህን ሁሉ ያካትታል ውድድሩ፡፡ ለመጀመሪያ ዙር ምን ያህል ተመዝጋቢ ትጠብቃላችሁ? የቋንቋና የሀገር ገደብ ስለሌለበት በመቶዎች የሚቆጠሩ ተመዝጋቢዎች እንደሚኖሩን እርግጠኛ ነኝ፡፡ የአንድ አካባቢ ተወዳዳሪዎች ቢያመዝኑስ? ሁለት ነገሮች አሉ፡፡ የዳኞቹ ስርጭት ሚዛናዊ ነው፡፡፡ መክፈቻውን እዚህ አዲስ አበባ አድርገናል። ሰሞኑን ኬንያ ሄደንም እናስተዋውቃለን፡፡ ጋዜጣዊ መግለጫችን በየቦታው እንዲዳረስ እናደርጋለን፤ በጋዜጠኛ ማህበራት ትስስራችን ጭምር፡፡ ከሁሉም የአፍሪካ አገራት ተወዳዳሪዎች ቢኖሩ ደስ ይላል።

የአንድ አካባቢ ብቻ እንዳይሆኑም አስበንበታል። እንደ አርታዒነቴ በቢቢሲ የነበረኝን ልምድ እጠቀማለሁ፡፡ እንደዛማ ካልሆነ የመላ አፍሪካ ውድድር መሆኑ ቀርቶ የኢትዮጵያ፣ የኬንያና የጥቂት ሀገሮች ብቻ ይሆናል - እንደ ሩጫ ውድድሩ፡፡ ሦስት ሳምንት (ካለፈው እሁድ ጀምሮ) ስላለን ጠንክረን እንሰራለን፡፡ ወዳንተ ልምጣና ቢቢሲን ከለቀቅህ በኋላ ምን እየሰራህ ነው? በ”ኢንተርናሽናል ሴንተር ፎር ጆርናሊስትስ” ፌሎውሽፕ አገኘሁ፡፡ የእድገትና የአፍሪካ ልማት ሥራዎች ያጓጉኛል፡፡ ጋዜጠኞችን በማሰልጠንም ተሳትፌአለሁ፡፡ ራሴንም አሰልጥኛለሁ፡፡ በብዙ የአፍሪካ ሀገራት ተንቀሳቅሻለሁ፡፡ ከዚያ ወደዚህ ወደ አፍሪካን ሚዲያ ኢኒሽየቲቭ መጣሁ፡፡ ለምን ነበር ቢቢሲን የለቀቅኸው? ቢቢሲ ውስጥ ለሃያ ዓመት ያህል ሠርቻለሁ፡፡ አውሮፓ ከምትፈልገኝ የበለጠ አፍሪካ ትፈልገኛለች።

ዋነኛ ምክንያቴ ይኼ ነው፡፡ በአፍሪካ ብዙ አማራጮች አሉ፡፡ ለንደን ብሆን ይህን አላገኝም። የአፍሪካ ጋዜጠኞች የኔን ልምድ ይፈልጋሉ፡፡ በኪስዋሂሊ ቋንቋም ሰርቻለሁ፡፡ በጣም ኬንያዊ፣ በጣም ምስራቅ አፍሪካዊ፣ በጣም መላ አፍሪካዊ የሆኑ የጋዜጠኛ ሥራዎች መስራት እችላለሁ፡፡ ይህ ጥሩ ፈታኝ ጊዜዬ ነው፤ ምክንያቱም አፍሪካዊ ፍላጐቴን እንድቀጥል ያደርገኛል፡፡ ቢቢሲን ስቀላቀል አፍሪካዊ አርታዒዎች ጥቂት ነበሩ፡፡ አሁን ቢቢሲን ጨምሮ በአልጀዚራ፣ በሲኤንኤንና በሌሎችም ሚዲያዎች ብዙ አፍሪካውያን አርታዒዎች አሉ፡፡ የራሳችንን ታሪክ ራሳችን ወደ መናገር ማደግ አለብን፡፡ እስቲ ስለራስህና ሙያህ ንገረኝ… በጉጉት የምሰራ ጋዜጠኛ ነኝ፡፡ አስተማሪ ነበርኩ። ለተወሰኑ ዓመታት አስተምሬአለሁ፡፡ የአፍሪካን ሙዚቃ እወዳለሁ፡፡ የአፍሪካን ጥበብ፣ እርሻ ወዘተ ለማየት ብዙ ተጉዣለሁ፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ግን ከረዥም ጊዜ በኋላ ነው ተመልሼ የመጣሁት፡፡ ያኔ ስመጣ መለስ አዲስ መሪ ነበሩ፡፡

በተረፈ ሁለት ልጆች አሉኝ፡፡ ወንዱ ልጄ ማስትሬት ዲግሪውን በፓሪስ እየሰራ ነው፡፡ ሴቷ ልጄ በእንግሊዝ የመጀመሪያ ዲግሪዋን እያጠናቀቀች ነው፡፡ ምን ቀረ? ባለቤቴ አስተማሪ ነች፡፡ በአፍሪካ ብቻ ከሠላሳ ሀገራት በላይ ለሥራ ተዘዋውሬአለሁ፡፡ ታዋቂ ኬንያዊ ነህ፡፡ ወደ ፖለቲካ የመግባት ፍላጐት የለህም? የለም ወደ ፖለቲካ አልገባም፡፡ ግን ተጽእኖ ፈጣሪ መሆን እፈልጋለሁ፤ ለውጥ ለማምጣት፡፡ በቢቢሲ አብረውኝ የነበሩ ጋዜጠኞች ወደ ፖለቲካ ገብተዋል፡፡ ፖለቲካ የተወሳሰበ ጫወታ ነው፡፡ በጋዜጠኝነት ሥራዬ ብዙ ፖለቲከኞችን አይቻለሁ። እኔ ግን በመገናኛ ብዙሃን ሥራዬ ለውጥ ማምጣት ነው የምፈልገው፡፡ ለፖለቲካ ሥልጣን መወዳደር አልሻም፡፡ በቢቢሲ የነበረህን ጥሩ ጊዜ አጫውተኝ… ብዙ ያለፈ ነገር ይናፍቀኛል፡፡ በ“ኔትዎርክ አፍሪካ” የነበሩ ባልደረቦቼ… ማክስ ጃሬት፣ ቤን ማሎር (አሁን በተባበሩት መንግስታት ነው ያለው)፣ ቦላ ሞስሩ (አሁንም ቢቢሲ ነች)፣ ሪክ ዌልስ፣ ሟቹ ክሪስ ቢከርተን፣ ሮቢን ዋይት፣ ነባር ሪፖርተሮቻችን ሶላ ኡድንፋ (አሁንም ከናይጄሪያ ለቢቢሲ የሚዘግበው)፣ ፍራንሲስ ንጉዋኒበ ከካሜሩን፣ እነዚህ ሁሉ ይናፍቁኛል። ያ ወቅት የቢቢሲ አፍሪካ አገልግሎት ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰበት ነበር፡፡

እነዚህ ሁሉ ከልቤ አይጠፉም፡፡ የተለየ አጋጣሚህን ብትነግረኝ? ካደረግኋቸው ቃለምልልሶች ሁሉ ከደቡብ ሱዳኑ ጆን ጋራንግ ጋር ያደረግሁት የተለየ ነው። በጣም ብልህ ነበሩ፡፡ ቃለምልልሱን የነፃ ትግል ውድድር መድረክ ነበር ያደረጉት፡፡ አስቂኝ ገጠመኜ ደግሞ ከቀድሞ የማላዊ ፕሬዚዳንት ባኪሊ ሙሉዚ ጋር ያደረግሁት ነው፡፡ ቃለምልልስ ለማድረግ ቤተመንግስት ተገኘሁ። በዋዜማው በቁንጅና ውድድር “ወይዘሪት ማላዊ” የተባለችውን ቆንጆ አነጋግሬአለሁ፡፡ ተቀጣጥረን ነው ወዳረፍኩበት ሆቴል የመጣችው፡፡ ፕሬዚዳንቱ ያንን ቃለምልልስ አዳምጠዋል። በቀጠሮአችን ቤተመንግስት ስንገናኝ “ስላየሁህ ደስ ብሎኛል፡፡ ከቆንጆዋ ጋር ሆቴል ውስጥ ምን ስትሠሩ ነበር?” ብለው አዝናንተውኛል። በጣም አስፈሪው ገጠመኝ ደግሞ በቡሩንዲ ቡጁንቡራ ነው።

ፕሬዚዳንት ሚልኪየር ንዳዳዬ እንደተገደሉ እዚያ ነበርኩ፤ የቴሌቪዥን ዜና ለመስራት፡፡ ሥራችንን ጨርሰን ወደ እንግሊዝ ለመመለስ ሦስት ሰዓት ሲቀረን የባህል ቅርሳቅርስ እየገዛሁ ሃይለኛ ተኩስ ተከፈተ፡፡ ሱቆች ውስጥ ተደበቅን፡፡ ከቆምኩበት ሁለት እና ሦስት ሜትር ርቀት ላይ አንድ ሚኒስትር ተገደሉ፡፡ ወደ ጋዜጠኝነት ሙያ እንድትገባ በአርአያነት ያነቃቃህ ጋዜጠኛ አለ? አደንቀው የነበረው ጋዜጠኛ እንኳን አልነበረም። ትምህርት ቤት እያለሁ ግን ሰር ዴቪድ ፍሮሰት የሚባል ነበር፡፡ ብዙ ያዳምጥሃል፤ አሁን አልጀዚራ ነው የሚሰራው፡፡ አንድ ቀን በትምህርት ቤት የዩኒሴፍ ኮንሰርት ላይ ሲናገር ሰምቼው፣ ንደዚህ መናገር እፈልጋለሁ ብዬ ተደንቄአለሁ፡፡ እስካሁንም በአርአያነት በአእምሮዬ ይመጣብኛል - ዴቪድ ፍሮስት፡፡

በምንድነው መታወስ የምትፈልገው? በአህጉሪቱ በመገናኛ ብዙሃን ላይ ለውጥ እንዳመጣ ሰው መታወስ እፈልጋለሁ፡፡ እስካሁን ምንም መጽሐፍ አልፃፍኩም፡፡ ቁጭ ብዬ አንድ ወይ ሁለት መፃህፍት የመፃፍ ሃሳብ አለኝ፡፡ በመጨረሻ የምታክለው ካለ እድሉን ልስጥህ… ከረዥም ጊዜ በኋላ ኢትዮጵያ በመምጣቴ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡ ልጆቼ የኢትዮጵያን ምግብ ይወዳሉ። በለንደንና በኬንያ አድነው ነው የኢትዮጵያን ምግብ የሚበሉት፡፡ አሁን ካንተ ጋር ከመገናኘታችን በፊት ልጄ ደውሎ እንዴት ነች ኢትዮጵያ ብሎኛል፡፡

Published in ህብረተሰብ

አስራ ሰባት አመታትን በህክምና ሙያ ውስጥ ላሳለፉት የውስጥ ደዌ ስፔሻሊስት ሐኪሙ ዶ/ር ተስፋዬ ደረሰ፡፡ ከአመት በፊት በአንጀት ቁስለት ህመም ተይዛ ወደሚሰሩበት ክሊኒክ በመጣችው ወጣት ላይ የደረሰውን ችግር ሁልጊዜም ያስታውሱታል፡፡ ወጣቷ ወደክሊኒኩ የመጣችው የሚሰማትን የቁርጠትና የራስ ምታት ህመም ለቀናት ከታገሰች በኋላ ነበር፡፡ ህመሙ አልሻልሽ ሲላትና ይባስ ብሎም የበላችው ሁሉ አልረጋ እያለ ሲያስቸግራት ለህክምና ወደ ክሊኒኩ ሄደች፡፡

ዶክተሩ ተገቢውን የላብራቶሪ ምርመራ ካደረጉላት በኋላ ህመሙ የአንጀት ቁስለት መሆኑን አረጋግጠው መድሃኒት ያዙላታል፡፡ መድሃኒቱን ቶሎ ገዝታ እንድትጀምር ይነግሯትና ከሣምንት በኋላ ሊያይዋት ቀጠሮ ይዘው ያሰናብቷታል፡፡ ከአራት ቀናት በኋላ ወጣቷ ወደ ክሊኒኩ የመጣችው በሰው ሸክም ነበር፡፡ በላብ ተዘፍቃ ቁና ቁና ትተነፍሣለች፡፡ ሐኪሟ ክው አሉ፡፡ አስቸኳይ ምርመራዎችን አድርገው በውስጥ የሰውነት ክፍሎቿ ላይ ጉዳት መድረሱን ተገነዘቡ፡፡ ይህ ሁኔታ የተከሰተው ደግሞ ያለአግባብ በወሰደቻቸው መድሃኒቶች ሣቢያ መሆኑንም ተረዱ፡፡

ዶክተሩ በማዘዣቸው ላይ ለታማሚዋ የፃፉት መድሃኒትና ህመምተኛዋ ለአራት ቀናት ስትወስደው የከረመችው መድሃኒት ፈጽሞ አይገናኝም፡፡ ጉዳዩ ግራ ቢያጋባቸው ለቤተሰቦቿ መድሃኒቱን ከየት ነው ያመጣችሁት የሚል ጥያቄ ሰነዘሩ፡፡ ቤተሰቦቿም መድሃኒቱን በአካባቢያቸው ካለ አንድ ፋርማሲ እንደገዙላትና “ፋርማሲስቱ” በነገራቸው መሠረት መድሃኒቱን ሲሰጧት እንደቆዩ ነገሯቸው፡፡ በሁኔታው እጅግ ሐዘን የተሰማቸው ዶክተሩ፤ ወጣቷን በክሊኒኩ አስተኝተው ክትትል ማድረጋቸውን ቀጠሉ፡፡ ወጣቷን ወደ ጤናማ ህይወት ለመመለስ ወራትን የፈጀ ህክምናና ከፍተኛ ወጪ መጠየቁንም ዶ/ር ተስፋዬ ይናገራሉ፡፡ ለዚህ ችግር መፍጠር ምክንያት የሆነው መድሃኒት ሻጭ ግን ያለምንም ተጠያቂነትና ያለምንም ችግር ሥራውን እያከናወነ ይገኛል፡፡

ይህ ሁኔታ ለዶክተሩ ትልቅ ራስምታት ሆኖባቸዋል፡፡ የሰውን ልጅ ህይወት ያህል ክቡር ነገር ላይ አደጋ ወይንም ጉዳት ሊያስከትል የሚችል ተግባር እያከናወኑ ያለምንም ተጠያቂነት መቅረት አግባብነት ያለው ተግባር አይደለም ይላሉ - ባለሙያው፡፡ በአገሪቱ ውስጥ ባሉ የመድሃኒት መሸጫ ቤቶች ላይ ጥብቅ ቁጥጥር በማድረግ ያለሞያቸውና ያለአቅማቸው በመድሃኒት ሽያጭ ተግባር ላይ ተሰማርተው የሚገኙትን ወገኖች ሃይ ማለት ተገቢ ነው ብለው ያምናሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት በአብዛኛዎቹ የመድሃኒት መሸጫ ቤቶች ውስጥ ያሉ “ፋርማሲስቶች” በዘመድ አዝማድ የገቡና ሙያውን ፈጽሞ የማያውቁ ናቸው ሲሉም ይናገራሉ፡፡ የልብ ህክምና ስፔሻሊስት የሆኑት ዶ/ር ተገኝ ተድላም ይህንኑ ሃሳብ ይጋራሉ፡፡ ውስብስብ ምርመራና ህክምና የሚፈልጉ እንደልብ ያሉ የሰውነታችን ክፍሎች እጅግ ከፍተኛ ጥንቃቄን የሚጠይቅ የመድሃኒት ማዘዝና ለህመምተኛው ማድረስ ሂደት ሊከናወንባቸው እንደሚገባ የሚናገሩት ዶክተሩ፤ ይህንን ሒደትም ሁሉም ባለሙያ እንደየሙያው ዘርፍና እንደችሎታው በኃላፊነት ስሜት ሁኔታ ሊፈጽመው ይገባል ይላሉ፡፡ ሁኔታው በተለይ በአሁኑ ጊዜ እጅግ አሳሳቢ ደረጃ ላይ እየደረሰ መሆኑን የህክምና ባለሙያዎቹ ይናገራሉ፡፡

በመድሃኒት ማዘዣው ላይ ከተፃፈው መድሃኒት ጋር ምንም ግንኙነት የሌላቸውን መድሃኒቶች ለህመምተኛው መስጠት፣ በማዘዣው ላይ ከተገለፀው ቁጥር በላይ ወይም በታች የሆኑ መድሃኒቶችን መስጠት፣ በግልጽ የተቀመጡ የመድሃኒት አወሳሰድ ትዕዛዛትን ለህመምተኛው አዛብቶ መንገር ወይም ጭርሱንም አለመንገር እና ተመሳሳዩ ነው ያለን በማለት ከዶክተሩ ትዕዛዝ ውጪ የሆኑ መድሃኒቶችን መሸጥ በአብዛኛው በመድሃኒት መደብሮች ውስጥ የሚገኙ “ባለሙያዎች” ተግባራት እየሆኑ መምጣታቸውን ሃኪሞቹ ይገልፃሉ፡፡ ይህንን የህክምና ባለሙያዎቹን አስተያየት ግን ተዘዋውረን በጐበኘናቸው የመድሃኒት መደብሮች ውስጥ ያሉ ፋርማሲስቶች አይቀበሉትም፡፡ በፋርማሲዎች ውስጥ በመድሃኒት ሽያጭ ሥራ ላይ ለመሰማራት በቅድሚያ በሙያው ተገቢውን ትምህርትና ስልጠና መውሰድ የሚያስፈልግ ከመሆኑም በላይ በዘርፉ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ፈተናን ወስዶ ማለፍ እንደሚገባም እነዚሁ ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡

በአብዛኛው የመድሃኒት መሸጫ ሥፍራዎች ላይ ሙያተኛ የሆኑ ሰዎች አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደሆኑ የሚናገሩት እነዚሁ ባለሙያዎች፤ በዘመድ አዝማድ የተቀጠሩ፣ ስለሙያው በቂ ዕውቀትና ልምድ የሌላቸው ሰዎች የሚሰሩባቸው መድሃኒት ቤቶች የሉም ለማለት አንደፍርም ይላሉ፡፡ እነዚህ ሰዎችም በፋርማሲው ውስጥ በሚኖራቸው ቆይታ ስለሚላመዱ ሽያጩን በጊዜ ሂደት ቢያከናውኑ አስገራሚ አይደለም በማለት ሃሳባቸውን ይገልፃሉ፡፡ ካዛንቺስ አካባቢ በሚገኝ አንድ ፋርማሲ ውስጥ በዚሁ ሥራ ላይ ተሰማርታ ያገኘኋትና ራሔል ታዬ የተባለችው ወጣት የዚሁ ሃሳብ ተጋሪ ነች። በአሁኑ ወቅት ከመንግስት ተቋማት ሌላ በግል ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥ እየሰለጠኑ የሚወጡ በቂ የፋርማሲ ባለሙያዎች ባሉበት ሁኔታ ሙያውን ያልተማሩ ሰዎች እየሰሩበት ይገኛሉ መባሉ እንደማይዋጥላት ገልፃ፤ ሥራውን እየሰሩም በመማር ላይ ያሉ “ፋርማሲስቶችን” እንደምታውቅ ተናግራለች፡፡

በአንድ ፋርማሲ ውስጥ ከሁለትና ሶስት በላይ የመድሃኒት ሽያጭ ሠራተኞች ስለሚኖሩም እርስበርስ በመረዳዳትና በመመካከር ሥራቸውን እንደሚያከናውኑ ገልፃለች። ከዚህ ይልቅ ለእሷና እንደእሷ ላሉ የሙያ ባልደረቦቿ አስቸጋሪው ነገር ዶክተሮች በመድሃኒት ማዘዣዎች ላይ የሚጽፏቸውን ጽሑፎች ማንበቡ እንደሆነም ራሔል ትናገራለች፡፡ የዶክተሮች ጽሑፍ እንደዛ መሆን ይኖርበታል የሚል መመሪያና ህግ በህክምና ሙያ ውስጥ ስለመኖሩ አልተማርኩም ግን አብዛኛዎቹ ዶክተሮች ሆነ ብለው ጽሑፎቻቸውን በዛ መልኩ በማበላሸት መፃፋቸው ከምን የመጣ እንደሆነ አይገባኝም፡፡ በምህፃረቃልና በኮድ የሚገለፁ ነገሮች እንዳሉ ይገባኛል፡፡ እንዲህ ግራ የተጋባ ጽሑፍ ግን እኔንም ብዙ ጊዜ ግራ ያጋባኛል ትላለች፡፡ ለህመምተኛው በሚስማማ መልኩ ተዘጋጅተው በሽታን ለማከም የምንጠቀምባቸው መድሃኒቶች በተገቢው ባለሙያ በአግባቡ ለህመምተኛው ካልደረሱና በአግባቡ በጥቅም ላይ ካልዋሉ ከጥቅማቸው ጉዳታቸው ያይላል፡፡ አንድ መድሃኒት ለተፈለገበት ተግባር በአግባቡ በጥቅም ላይ ከዋለ ፈዋሽነቱ አያጠራጥርም፤ የትኛውም ሐኪም መድሃኒቶችን ከማዘዙ በፊት ሊያከናውናቸው የሚገባ ቅድመ ምርመራዎች አሉ።

በሽታ አምጪው ህዋስ በተገቢው ቤተሙከራ ተመርምሮ እንዲታወቅ በማድረግ ለበሽታው መድሃኒት ይታዘዛል፡፡ ሐኪሙ መድሃኒቱን የሚያዘውም በመድሃኒት ማዘዣ (Prescription) ነው፡፡ ይህ የመድሃኒት ማዘዣ መድሃኒቱን ለህመምተኛው የሚያዘው ሐኪምና የፋርማሲ ባለሙያውን የሚያገናኝ ድልድይ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የመድሃኒት ማዘዣዎች ከህግና ከሙያ ሥነምግባር አንፃር ተጠያቂነት ሊያስከትሉ የሚችሉ ህጋዊ ሰነዶች ናቸው፡፡ ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ያገኘናቸው መረጃዎች እንደሚያመላክቱት፤ መድሃኒቶችን ለህሙማን የሚያድሉ ባለሙያዎች መድሃኒቶቹ የሚያስከትሏቸው አላስፈላጊ የሆኑ ውጤቶችን ለህሙማኑ በግልጽ የማሳወቅ ግዴታ አለባቸው፡፡ አብዛኛዎቹ መድሃኒቶችን በምንም አይነት ሁኔታ ያለሐኪም ማዘዣ መሸጥ በህግ ያስቀጣል፡፡ በተለየ መልኩ ደግሞ ሱሰኝነትን አሊያም የመድሃኒት ጥገኛ መሆንን የሚያበረታቱ የመድሃኒት ዓይነቶች በልዩ የመድሃኒት ማዘዣ ብቻ በጥቅም ላይ እንዲውሉ ያደርጋሉ፡፡ እነዚህን አይነት መድሃኒቶች ለማዘዝ የሚችሉትም የስፔሻላይዝድ ዕውቀት ያላቸው ሐኪሞች ብቻ ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ምንም አይነት ማዘዣ የማያስፈልጋቸው መድሃኒቶች አሉ።

እነዚህ መድሃኒቶች ህመምን ከማስታገስ የዘለለ ጠቀሜታ የማይሰጡ በመሆናቸው የከፋ ችግር አያስከትሉም፡፡ ለምሣሌ ራስ ምታት፣ ጉንፋን፣ የመሳሰሉትን ማለት ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ቀላል የሚባሉ የበሽታ ምልክቶች ምናልባትም ትላልቅ የውስጥ የጤና ችግሮችን ሊያስከትሉ ስለሚችሉ የፋርማሲ ባለሙያው መድሃኒቶቹን ያለማዘዣ በሚሸጥበት ወቅት ለህመምተኛው መድሃኒቶችን እስከዚህ ቀን ድረስ ተጠቅመህ መፍትሔ ካላገኘህ ወደ ጤና ተቋማት መሄድ ይኖርብናል የሚል ሞያዊ ምክር መስጠት ይጠበቅባቸዋል፡፡ በህክምናው ሞያ ውስጥ ተሰማርተው የሚገኙ የጤና ባለሙያዎቹ እንደሚናገሩት፤ ይህንን የማድረግ አቅምና ችሎታ ያለው የመድሃኒት ቤት ባለሙያ ማግኘቱ አስቸጋሪ ከሆነ ሁኔታው እውነትም እጅግ አሳሳቢ ሆኗል ማለት ነው፡፡

Published in ዋናው ጤና

“ለአንድ ዲፓርትመንት ብለን የዩኒቨርሲቲውን ካሌንደር አንቀይርም” የዲፓርትመንቱ ኃላፊዎች በአዳማ ዩኒቨርሲቲ የሲቪል ምህንድስና የ3ኛ ዓመት ተማሪዎች የወጣውን የፈተና ፕሮግራም በመቃወም ረቡዕ ጠዋት በዩኒቨርሲቲው ውስጥ ሰላማዊ ሰልፍ አደረጉ፡፡ ተማሪዎቹ “መንግሥት በመደበልን ጊዜና በጀት የመማር መብታችን ይከበር” “There is no exam without education” እና የመሣሠሉ መፈክሮችን አሰምተዋል፡፡ “የዘንድሮው ምዝገባ በሦስት ሳምንት ዘግይቶብናል፣ ከተመዘገብንም በኋላ ሁለት ሳምንት ዘግይተን ነው ትምህርት የጀመርነው” በማለት ቅሬታቸውን ያሰሙት ወደ 300 የሚጠጉት የሲቪል ምህንድስና የሦስትኛ ዓመት ተማሪዎች “አራት ሚድ ተፈትነን ከፋሲካ በዓል ስንመለስ አራት ሜጀር ኮርሶችን አንዳንድ ቻፕተር ብቻ የተማርናቸው አሉ፣ አስተማሪዎች በሥነ-ሥርዓቱ ስለማይገቡ አሁን ጊዜው ሲደርስ ለመጨረስ ቅዳሜ ማታ ሳይቀር እየተዋከብን እንማራለን፣ አንድ ላይ የማይወሰዱ ኮርሶችን በአንድ ላይ እንወስዳለን፣ ቤተ-ሙከራ (ላብ) አናውቅም፤ እስከ አርብ ተምረን ሰኞ ፈተና ልንቀመጥ አይገባም” የሚሉና መሰል ጥያቄዎችን አቅርበው የፈተናው ጊዜ ሊራዘምላቸው እንደሚገባ ጠይቀዋል፡፡

“ተሰብሰቡና እናነጋግራችኋለን” ተብለው “ፓርላማ” በተባለው አዳራሽ ውስጥ የተሰበሠቡት ተማሪዎች ከቆይታ በኋላ ሦስት የዲፓርትመንቱ ኃላፊዎች መጥተው ለማነጋገር ሲሞክሩ ብዙ አለመግባባቶች እንደነበሩ በስብሰባ አዳራሹ ተገኝተን ታዝበናል፡፡ የዲፓርትመንቱ ኃላፊ “ችግሩን ለማቅረብ በጣም ዘግይታችኋል” ተመዝግባችሁ ያልጀመራችሁት ኮርስ ካለ ተውት፣ ጀምራችሁ ያልጨረሳችሁት ኮርስ ካለ ጊዜ ፈልገን ትማራላችሁ፣ የዩኒቨርሲቲው ካላንደርና የፈተና ፕሮግራሙ ግን ለአንድ ዲፓርትመንት ተብሎ አይቀየርም በማለታቸው ተማሪዎቹ ቁጣቸውን በጩኸት ገልጸዋል፡፡ “የፈተና ፕሮግራሙ ለአራተኛ ጊዜ ተቀያይሯል፤ ይህ ለምን እንደሆነ አናውቅም” ስምንት ኮርስ እየወሰድን ጊዜው አጥሮብናል” ያሉት ተማሪዎቹ በሌላ ዩኒቨርሲቲ ዋናውን ፈተና ሰኔ 16 ነው የሚጀምሩት፤ እኛ ግን ገና ተምረን ሳንጨርስ አርብ ጨርሳችሁ ቅዳሜ ውጡ ልንባል አይገባም” በማለት ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡ አንድ ተማሪ ተነስቶ ባደረገው ንግግር “ምዝገባን ያዘገየው ሌላ ሰው፣ የችግሩ ሰለባ የሆንነው እኛ ነን ሁሉንም ችግር ያላጠፋነውን ሁሉ እንዲንሸከም የምታደርጉት ተማሪውን ነው” በማለት ቅሬታውን ገልጿል፡፡

ተማሪው አክሎም “እኛ እናንተ ምን ኃላፊነት እንዳላችሁ አናውቅም፤ ምንም ስትከታተሉ አይተናችሁ አናውቅም፣ ችግሩን አዘግይታችኋል የምትሉት ትክክል አይደለም፣ የሚሰማን አጥተን ነው እንጂ ስንጮህ ነው የቆየነው፤” አሁንም ቢሆን ጊዜው ተራዝሞ ኮርሶቻችንን ጨርሰን የምንፈተንበት መንገድ ይፈለግልን” ያለው ተማሪው “በዚህ ሁኔታ ከተፈተንን ኪሳራው የተማሪው፣ የዩኒቨርሲቲውና ብሎም የሀገሪቱ ነው” ሌላ ተማሪ በበኩሉ “እኔ በሦስት ዓመት ውስጥ እንደ ምህንድስና ተማሪ ማወቅ የሚገባኝን አውቄያለሁ ብዬ አላምንም” ካለ በኋላ በግቢው አስተማሪ ማስተማርም አለማስተማርም መብቱ እንደሆነ፣ አንዳንድ አስተማሪዎች ፈተና 15 ቀን ሲቀረው እየመጡ እንደሚያጣድፉ፣ ዩኒቨርስቲው ይህን እንደማይከታተልና ችግሩ ሰለባ እየሆነ ተማሪው እንደሆነ በአፅንኦት ተናግሯል፡፡ “አሁን ሰኔ ስምንት እንድንወጣ የሚደረገው በበጀት እጥረት ነው፤ እኛ እንደ ማንኛውም ዩኒቨርሲቲ “ኮስት ሼሪንግ” የምንፈርመው ከመስከረም እስከ ሰኔ 30 ነው፡፡ ስንገባም ጥቅምት አምስት ነው ወደ ጊቢ የመጣነው፡፡ ስለዚህ መንግሥት የመደበልን ጊዜና በጀት እስከ ሰኔ 30 የሚያቆየን በመሆኑ ቀስ ብለን ተረጋግተን ልንፈተን ይገባል” ብሏል፡፡

ኮስት ሼሪንግ የፈረሙበት ፎቶ ኮፒ እጃችን ላይ ይገኛል፡፡ “ሌላው ዩኒቨርሲቲ የራሱ አካሄድ አለው፡፡ አዳማም በትምህርት ሚኒስቴር በተሰጠው ካሌንደር ነው የሚሠራው” ያሉት የዲፓርትመንቱ ኃላፊ “አሁን ችግር ያላችሁት የፈተና ፕሮግራሙ ነው፤ እሱ ላይ ተናገሩ እንጂ ጠቅላላ ችግር አታውሩ” በማለት ቁጣ በተቀላቀለው አጽንኦት ተማሪዎቹን ገስፀዋል፡፡ ይሁን እንጂ ተማሪው ኃሀላፊውን ቁጣ ወደ ጐን በመተው “አንድ ኮርስ በሳምንት ብቻ የምንጨርስበት ሁኔታ አለ፤ እኛ ዴቨሎፕ ሳናደርግ ነው የምንፈተነው፤ ዜጋን ለማዳን ከተፈለገ የማይለወጥ ነገር የለም፡፡ በትምህርቱና በፈተናው መሀል ክፍተት ተሰጥቶን እንፈተን” በማለት ጥያቄያቸውን ቀጥለዋል፡፡ “እኔ ተማሪ በነበርኩበት ጊዜ መማር የሚገባኝን ያህል አልተማርኩም፣ አስተማሪም ከሆንኩ በኋላ ለተማሪዎቼ በአግባቡ አስተምሬያለሁ ብዬ አላምንም” በማለት ለተማሪዎች ምላሽ መስጠት የጀመሩት ሌላው ኃላፊ፤ ይህ ከእኔም ስንፍና፣ ከዩኒቨርሲቲውም ችግር አሊያም በሀገሪቱ ካሉት በርካታ ገደቦች ሊሆን ስለሚችል አሁን ባለው ሁኔታ ቶሎ ቶሎ ጨርሳችሁ ተፈተኑ” ማለታቸው ተማሪዎችን የበለጠ አስቆጥቶ ነበር፡፡ በአዳራሹ ውስጥ ጭቅጭቁ እየከረረ በመሄዱ አንድ ተማሪ አንድ የተሻለ የሚለውን ሐሳብ አቀረበ፤ “አንድ ኮርስ አሳይመንት ሠርተናል፤ እሱ ከመቶ ይታይና መፈተኑ ይቅርብን፡፡

ይህም የሚጠበውን ጊዜ ይቆጥባል ከዚያ በተረፈ ቢያንስ አንድ ቅዳሜ ይጨመርልንና ትንሽ ጋፕ ይኑረን” በማለቱ ኃላፊዎቹ እየከበዳቸውም ቢሆን ለመቀበል ተገደዋል፡፡ ተማሪዎቹ እንደሚሉት በዩኒቨርሲቲው ብዙ ችግር እንዳለባቸውና ፕሮፌሰር ማጁንዳ የተባሉ የቢዩልዲንግ አስተማሪ በሰጡት ግሬድ ስላልታመነበት ከአስተዳደር ክፍሉ በተነሳ ጭቅጭቅ አስተማሪው አጠቃላይ የተማሪዎቹን ውጤት ይዞ ወደ ህንድ በመሄዱ ውጤት በጊዜ ሊታወቅ ስላልቻለ ምዝገባው ለሦስት ሳምንት መዘግየቱን ተናግረዋል፡፡ ኃላፊዎቹም ይህን አምነው አስተማሪውን በኢሜልም በስልክም አነጋግረን ሊታረም ባለመቻሉ ከስራው ማሰናበታቸውንና የምዝገባው ጊዜ መዘግየቱን ተናግረዋል፡፡ “እኛ በአግባቡ አልተማርም ያልዘሩብንን ሊያጭዱ ይሞክራሉ፡፡ ይኼ ለዚህች አገር ውድቀት ከፍተኛ ቁልፍ ነው” ያሉት ተማሪዎቹ ትምህርት ሚኒስቴርና የሚመለከተው አካል ዩኒቨርሲቲውን እንዲቆጣጠረውና እንዲፈትሸው አሳስበዋል፡፡ “ችግሩ የእኛ ዲፓርንመንት ብቻ ሳይሆን የሁሉም ነው” ያለችው አንዲት የዲፓርትመንቱ ተማሪ እኛ ከማወቅ ሳይሆን ከመጨረስ አኳያ ነው እየተዋከብን ያለነው፤ መንግስት ችግራችንን ይወቅልን” ስትል ተናግራለች፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ተማሪዎቹ ያለባቸውን ችግር ችለው እንዲፈተኑና በተባለው ጊዜ ግቢውን እንዲለቁ ትዕዛዝ ተሰጥቶ ስብሰባው ቢበተንም ተማሪዎቹ ቅሬታ እንዳለዙ ሲበታተኑ ለመታዘብ ችለናል፡፡

ከብዙ ጊዜ ጀምሮ ስለአንድ በዕብደቱ ስለሚታወቅ የኢራን ሰው የሚተረት አንድ ወግ አለ፡፡ ይህ ዕብድ በዋና ዋና መንገዶች ላይ ባሉ አደባባዮች ዙሪያ ብቻ ነው የሚገኘው፡፡ አንድ አደባባይ አጠገብ መጥቶ ዙሪያውን መዞር ከጀመረ መቆሚያ የለውም፡፡ መሽቶ ጨልሞበት ወደ ማደሪያው እስከሚሄድ ድረስ መዞሩን ይቀጥላል፡፡ “ወዴት ትሄዳለህ?” ይሉታል ሰዎች ጠዋት፡፡ “ወደ አደባባዬ ነዋ!” ይላል፡፡ “አደባባዩን ማን ሰጠህና?” “እኔ የተፈጠርኩት ለአደባባይ መሆኑን አታውቁም? አደባባይስ የተፈጠረው ለእኔ መሆኑን አታውቁም?” እያለ እየዘፈነ ይሄዳል፡፡ ዕብዱ፤ ዋንኛ ጠባዩ ሰው አለመንካቱ ነው፡፡ “ሰውን ትሰድበዋለህ እንጂ አትመታውም” ይላል፡፡

“ለምን?” ይሉታል ሰዎች፤ ሊያጫውቱት፡፡ “የሰው ልጅ ሲደበደብ ይደድባል፡፡ ሲሰደብ ግን ብልጥ ይሆናል” “እንዴት?” “ለመልስ የሚሆን ስድብ ሲያዘጋጅ ማሰብ ይጀምራል፡፡ የስድብ ትምህርት ቤት ስለሌለ፤ ኦርጅናሌው የስድቡ ባለቤት እሱ ይሆናል” ሌላው የዚህ ዕብድ ጠባይ አንድ ጠዋት መናገር የጀመረውን ነገር በጭራሽ አይለውጠውም፡፡

ለምሳሌ አንድ ጠዋት፤ “የማይጮህ ህዝብ ምላሱ መቆረጥ አለበት!” ይላል፤ ካልን ቀኑን ሙሉ፤ “የማይጮህ ህዝብ ምላሱ መቆረጥ አለበት” ሲል ይውላል፡፡ በሚቀጥለው ጠዋት፤ “ሞኝ ያሥራል ብልጥ ይማራል!” ይላል፡፡ “The smarter prisoner yet learns. The fool governer forever imprisons” እንደ ማለት) ቀኑን ሙሉ ይቀጥላል፡፡ ደሞ ሌላ ጠዋት፤ “የሚዘምሩ ወፎች አሉ፡፡ የሚያርፉበት፤ ጐጆ እሚሠሩበት ዛፍ ግን የላቸውም” ይላል፡፡ እንዲህ እንዲህ ሲል ከርሞ አንድ ቀን ጠዋት፤ “ንጉሡ ጭንቅላታቸውን በርዷቸዋል!!” እያለ እየደጋገመ መጮሁን ቀጠለ፡፡ የአገሪቱ ፀጥታ አስከባሪ ኃላፊ፤ “አሁንስ አበዛው!” ብለው አንድ ፖሊስ አስገድዶ እንዲያስረው ላኩበት፡፡ ዕብዱ መሮጥ ጀመረ፡፡ “የዕብድ ጉልበት አያልቅም” ይባላል፡፡ ፖሊሱ ግዴታው ነውና የሚፈፅመው እየሮጠ መከተሉን ቀጠለ፡፡ ዕብዱ ያደባባዩን ዳር ዳር ይዞ ዙሪያውን ነው የሚሮጠው።

እንደወትሮው ከመስመሩ አይወጣም፡፡ ወደአደባባዩ ውስጥም አይገባም፡፡ ፖሊሱ ደከመውና ቆመ፡፡ ይሄኔ ዕብዱ ከት ከት ብሎ ሳቀና፤ “ሞኝ በመሆንህ ነው እንጂ የት እሄድብሃለሁ? ከአደባባይ የበለጠ እሥር ቤት የት አለና ነው? ይልቅ ሰው ከአደባባይ እንዳይጠፋ ማረግ ነው የሚሻለው!” አለ ይባላል፡፡

                                                               * * *

አካባቢያችንን እንፈትሽ፡፡ አደባባዩ ምሽግ ያደረገውንና ዕውነት የሚናገርበትን እንለይ፡፡ አገራችንን እናጥና፡፡ ዙሪያ ገባውን ማትሮ ጣራውንም ግርጌውንም በዐይነ ቁራኛ አይቶ ነው፡፡ የዘንድሮ ጉዞ፡፡ እንኳን የካዝና ግድግዳ የአዕምሮ ሽንቁርም አደገኛ ነው፡፡ “በራቸውን ሳይዘጉ ሌባ ሌባ ይላሉ” አለች አሉ ውሻ፡፡ ሌባው ቢያዝም እንኳ አሁንም በሩ ክፍት ከሆነ ለአዲስ ሌባ ምቹ መሆኑ አይቀርም፡፡ ህጉ ወደ ኋላ አይሰራም፤ ተመስገን ነው፤ በሚል በጊዜ ሰርቄ አምልጫለሁ፤ የሚልንስ እንዴት እንደምናስተናግደው ማጤን አለብን፡፡ ከጥንት ጀምሮ በውል እንደሚታወቀው ለሀገሩ ህልውና፣ ለሉዓላዊነቱ፣ ቀናዒ ህዝብ ነው ያለን። “ያልጠረጠረ ተመነጠረ” የሚለው ወዶ አይደለም፡፡ ተደጋግሞ ለጥቃት አጋልጦት ነው፡፡

አለ ነገር አለ ነገር ቁልቁለቱን ወርደን ወንዙን ስንሻገር”፤ ይላል አርቆ እያሰበ፡፡ ከላይ እስከታች፣ ነገር አለ፣ እያለ እየተጠራጠረ፣ መጓዝን የመረጠ ነው፡፡ መጠራጠርን እንተው ቢባልም እሚጠራጠር ካለ መጠርጠር መጥፎ አደለም፡፡ አንዱ ጓዳ ውስጥ ሲያንጐዳጉድ ሌላው ሳሎን እንደሚወራች አሊያም በተገላቢጦሹ ሊከሰት ይችላል፡፡ የውስጥ ችግሮቻችንን ዐይተው ባላንጦቻችን እንደሚጠራሩ መቼም ቢሆን መዘንጋት አይገባም። “ለነገር ይሁን ለፍቅር” ለዩ፤ ይላሉ አበው፡፡ ስለተጠራሩብን ጆሮአችንን በየአቅጣጫው ማቅናት ይጠበቅብናል፡፡ “እዚያ ማዶ ሆኖ ክፉ ሰው ተጣራ፤ እዚህ ማዶ ሆኖ ክፉ ሰው ወይ አለው፤ ጐበዝ ተጠንቀቁ፣ ይህ ነገር ለኛ ነው!!” ማለትም የአባት ነው፡፡ “ብቻውን የበላ ብቻውን ይሞታልን” አለመርሳትም ብልህነት ነው፡፡ በጥቃቅን መብራት በበራባቸው ነጥብ - ቦታዎች፣ በተመረጡ ወንጀሎች፣ በተመረጡ ሰዎች ላይ ስናተኩር ያልተመረጡትን ማየት ይሳነናል፡፡ ከመካከላቸውም ንፁሃኑን መለየት ይቸግረናል፡፡ ሁለመናችንን እንይ ጐበዝ፡፡ ሁሉም ከተበላሸ ወይም ሁሉም ከተሳሳተ ችግር ነው “በገንፎ የተሠራ ጥርስ፤ አያስቅ፤ አያስፍቅ” ማለት ሥረ - ነገሩ ይሄው ነው፡፡

Published in ርዕሰ አንቀፅ

“ሙስናን የሚያስተምረው ራሱ ገቢዎችና ጉምሩክ ነው” - ነጋዴዎች አብዛኛው ነጋዴ በፍርሃት ከአገር እየወጣ ነው ለነጋዴው ግዴታው እንጂ መብቱ አይነገረውም ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከከፍተኛ ግብር ከፋዮች ጋር ትላንት ረፋዱ ላይ ባደረገው ውይይት ሙስናን ለነጋዴው የሚያስተምረው ገቢዎችና ጉምሩክ እንደሆነ ከፍተኛ ግብር ከፋዮች ተናገሩ፡፡ በአዲስ አበባ የስብሰባ ማዕከል በተደረገው እና በገቢዎችና ጉምሩክ የከፍተኛ ግብር ከፋዮች ሥራ አስኪያጅ በአቶ አሰፋ ወሰን አለነ፣ በባለስልጣኑ የኦፕሬሽን ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር በአቶ ካይዳኪ ገዛኸኝ እና በባለስልጣኑ የለውጥና ሞደርናይዜሽን ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር በአቶ አብርሃም ንጉሴ አወያይነት በተካሄደው ውይይት ነጋዴዎች በሰጡት አስተያየት፤ “የጉምሩክ ሠራተኞች በራስ መተማመን የላቸውም፣ በየደረጃው ውሳኔ የመስጠት አቅም አጥተዋል፣ መረጃ ፈጥነው ለመስጠት ይቸገራሉ” በማለት ይህም ለነጋዴውም ሆነ ለአገሪቱ ከፍተኛ ጉዳት መሆኑን ገልፀዋል፡፡

በአገሪቱ እጅግ በርካታ መልካም ፖሊሲዎች ቢኖሩም አፈፃፀም ላይ በጣም ከፍተኛ ችግር እንዳለባቸው የገለፁት ነጋዴዎቹ፤ እነዚህ የአፈፃፀም ችግሮች ለሙስና በር ከፋች በመሆናቸው መጀመሪያ መጥራትና መጠረግ ያለበት እዛው ገቢዎችና ጉምሩክ ውስጥ ያለው አቧራ ነው ብለዋል፡፡ “በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዕቃ ግዢ ፈጽመን ደረሰኝ ብንጠይቅ ሊሠጠን ባለመቻሉ ስንከራከር ገቢዎችና ጉምሩክ ሄደህ ክሰሳ እንባላለን፤ እነዚህ ሰዎች ገቢዎችና ጉምሩክ የሚሠራ ተባባሪ እንዳላቸው ግልጽ ነው” ያሉት አንድ ከፍተኛ ግብር ከፋይ፤ ይህን ሁሉ እየተመለከትን ነጋዴ መሆናችንን እየጠላ ነው ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን በመቶ ቢሊዮን የሚቆጠር ግብር በአጭር ጊዜ መሰብሰቡንና ለዚህም ውጤት አሁን ተጠርጥረው በእስር ላይ የሚገኙት የባለስልጣኑ ዳይሬክተሮች ትጋት ትልቅ ድርሻ እንዳለው ያወሱት ሌላ ከፍተኛ ግብር ከፋይ በበኩላቸው፤ እኒህ ግለሰቦች በጥፋት ተጠርጥረው በታሰሩበት ወህኒ ቤት ድብደባና እንግልት መፈፀሙ በጣም እንደሚሰቀጥጣቸው ተናግረዋል፡፡ ነጋዴው አክለውም “ሰው ሆኖ የማይሳሳት የለም፣ ሙስና በጣም ያሳስታል፣ አጥፍተውም ይሆናል፤ ነገር ግን ውለታቸው መዘንጋት ስለሌለበት በእስር ላይ እያሉ መብታቸው ሊከበር ይገባል” ካሉ በኋላ በጥፋታቸው አይቀጡ ማለቴ አይደም ብለዋል፡፡

“እግር ኳስን እንመልከት፤ ይሄ ሁሉ ብር እየወጣባቸው አንዴ እንኳ አሸንፈው አያውቁም፤ የመብራት ነገርም እንደዛው ነው” ያሉት ግብር ከፋዩ፤ ትንሽ ጥፋት ሲያጠፉ ከፍተኛ ልምድ እና እውቀት ያላቸውን ከጥፋታቸው አርሞ እንደመመለስ፣ ከስራ እያስወገዱ በአዳዲስ መተካት ለዚህች አገር ከፍተኛ ጉዳት እንደሆነ በአጽንኦት ተናግረዋል፡፡ ከቀረጥ ነፃ የሚገቡ እቃዎች ላይ፣ በዲቪደንት ፈንድ እና በሲሚንቶ ሥራ ላይ ስለተከሰተው ችግር ሰፊ ሃሳብ ያቀረቡት ሌላው ከፍተኛ ግብር ከፋይ፤ በታክስ ስርዓት ላይ ህጐች ሲወጡ ወደፊት ሊያመጣ የሚችለው ተጽእኖ ተገምቶ መሆን እንዳለበት ጠቁመው፤ የወጡት ህጐችም ቢሆኑ ጥሩዎቹ ቀጥለው የማያሰሩት መወገድ አሊያም መከለስ እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡ “ህገ-ወጦች ወደ ሙስና ሲሮጡ እናንተ የምትከታተሉት ግን ህጋዊ ነጋዴዎቹን ነው” ያሉት ሌላው ነጋዴ፤ ህጋዊው ምን እንደሚሸጥ፣ እንዴት እንደሚሸጥ፣ ገቢና ወጪው ምን እንደሆነ ስለምታውቁ ከዚያ ዝንፍ እንዳይል ትከታተላላችሁ” ብለዋል፡፡ ህገ -ወጦች ግን አካሄዳቸው የጨለማ ስለሆነ እነሱን አትከታተሉም ሲሉ ወቅሰዋል፡፡

ነጋዴውን ወደ ታክስ ሥርዓቱ ማስገባቱ አስፈላጊ ቢሆንም ወደ ታክስ እንዲገባ የተደረገበት መንገድ በጣም የተሳሳተ መሆኑን የተናገሩት ሌላ ተሳታፊ ነጋዴ፤ ገቢዎችና ጉምሩክ የመንግስት ሠራተኛን የአገር ተቆርቋሪ፣ ነጋዴውን ደንታ ቢስ አድርጐ እየፈረጀ በመቆየቱ በባለስልጣኑና በነጋዴው መካከል ከፍተኛ ክፍተት ተፈጥሮ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ ባለስልጣኑ ግብርን በጉልበት ለማስገበር ነጋዴውን ሲያስር እና ሲያንገላታ የነበረበት መንገድ በባለስልጣኑ ላይ ጥላቻን ዘርቶ እንደነበር የገለፁት እኚህ ነጋዴ፤ ኦዲተሮቹም የባለስልጣኑም ሠራተኞች ጉልበተኞች እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡ “ነጋዴው ለኦዲት የሚያቀርበው ትክክለኛ ሂሳብ እንኳን ቢሆን እኔ ካላመንኩበት አልቀበልም እስከማለት መብት አላቸው” ያሉት ነጋዴው፤ ይህ የሚያሳዝንና ነጋዴው ከዘርፉ እንዲወጣ የሚገፋፋ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ነጋዴው አክለውም ምን ያህሉ ኦዲተሮች ንፁህ እንደሆኑም አላውቅም ብለዋል፡፡

ነጋዴው ለፍቶና ጥሮ ባመጣው ሀብት አጭበርብረሃል እየተባለ በመሆኑ አብዛኛው ነጋዴ ለድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ እየቀጠረ በፍርሃት ከአገር እየወጣ መሆኑንም ጨምረው ተናግረዋል፡፡ በግብር ከፋዩና ሰብሳቢው መካከል እንዲሁም በግብር ሰብሳቢው ሥራ አስፈፃሚዎችና በበላይ ባለስልጣናት መካከል የመረጃ ክፍተት መኖሩን፣ መረጃ በጽሑፍ ከሚሰጥበት በቃል የሚሰጥበት ጊዜ መብዛቱን፣ ለነጋዴው በአብዛኛው የሚነገረው ግዴታው እንጂ መብቱ አለመሆኑን የጠቆሙት ሌላው ከፍተኛ ግብር ከፋይ፤ መረጃ ከጽሑፍ ይልቅ በቃል መሰጠቱ ለሙስና ከፍተኛ በር እንደሚከፍት ገልፀው፤ ባለስልጣኑ እርምጃ መውሰድ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ የኢ-ታክስ ሲስተም መዘርጋቱ መልካም መሆኑን፣ ነገር ግን መረጃ የመቀበል አቅሙ አነስተኛ በመሆኑ መላ ሊፈለግለት እንደሚገባም በውይይት መድረኩ ተነስቷል፡፡

አንድ ነጋዴ ኦዲት ለማስደረግ ወደ ኦዲተር ሲቀርብ በዶክመንቶቹ ላይ ክፍተቶች ካሉ “ይሄ ይሄ በዚህ ይስተካከል” ብሎ ኦዲተሩ በመግለጽ ነጋዴው አስተካክሎ እዛው መክፈል ሲገባው “ይሄ ትክክል አይደለም” ተብሎ እንዲመለስ እየተደረገ የዘጠኝና የአስር አመት ውዝፍ ግብር ክፈል እያሉ ነጋዴውን ማስጨነቅ አግባብ አለመሆኑ ተገልጿል፡፡ ገቢዎችና ጉምሩክ አንድን ድርጅት ደውሎ በ10 ቀን ውስጥ ኦዲት ስለምትደረግ ተዘጋጅ ማለቱ አግባብ እንዳልሆነ በመጠቆምም በስልክ የሚተላለፍ ትዕዛዝ ለሙስና ድርድር በር እንደሚከፍትና ባለስልጣኑ በደብዳቤ ማሳወቅ እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ “አንዳንዴ ችግሮች ሲፈጠሩ ግብር ይግባኝ ለመሄድ የግብሩን 50% ማስያዝ ይጠበቅብናል” ያሉት ሌላው ግብር ከፋይ፤ ከፍተኛ ግብር ከፋዮች የሚከፍሉት ከፍተኛ ስለሆነ የዛን ግማሽ ማስያዝ ይከብዳቸዋል፡፡ ለዚህም ወደ ¼ኛ ዝቅ ቢል የተሻለ ነው ሲሉ አስተያየታቸውን ገልፀዋል፡፡

ሌላው ግብር ከፋይ በባለስልጣኑ ፕሮፌሽናል ሰዎች እንደሌሉ ጠቁመው “እኔ ካሽ ሬጅስተር ማሽን ይዤ ስሄድ የምን ብረት ነው ያለኝ ሰው አጋጥሞኛል” ካሉ በኋላ፤ ባለስልጣኑና ግብር ከፋዩ እንዲናበብ በየቦታው የተሰጣቸው ሃላፊነት የሚመጥኑ ፕሮፌሽናል ሰዎች ሊመደቡ ይገባል ብለዋል፡፡ የባለስልጣኑ መስሪያ ቤት የስራ ሃላፊዎች ከተወያዮቹ ለተነሱት አስተያየቶችና አንዳንድ ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡ ሲሆን እስካሁን የዚህን አመት ግብር ያልከፈሉ የከፍተኛ ግብር ከፋይ ነጋዴዎችም በቀሪዎቹ ሁለት ወራት ውስጥ አጠናቀው እንዲፍሉ አሳስበዋል፡፡ በተወያዮቹ ከህግ እና ከአመራር አኳያ የተነሱትን ጉዳዮች በተመለከተ፣ የባለስልጣኑ የሥራ ሃላፊዎች ክፍተቶቹ መኖራቸውን አምነው በዘላቂነት ችግሮቹን ለመቅረፍ የማሻሻያ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ከነዚህ የማሻሻያ ስራዎች መካከልም የህግ ዝግጅቶችም በዋናነት እንደሚካተቱ የጠቆሙት ሃላፊዎቹ፤ በቅርቡ የጉምሩክ ህግን ባለስልጣኑ አዘጋጅቶ በመጨረስ ወደ አጽዳቂው አካል ለመምራት በዝግጅት ላይ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

በቀጣይም በገቢ ዘርፍ የሚታዩ የአሠራር ጉድለቶችን በዘላቂነት ለመቅረፍ ገቢን የተመለከቱ አንቀፆች ብቻ የተካተቱበት ህግ ለማዘጋጀት እየተሰራ መሆኑንና በዝግጅቱ ወቅት ነጋዴዎችን ጨምሮ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት እንደሚሳተፉበት ተመልክቷል፡፡ ዲቪደንት ታክስን በተመለከተ ለተነሱት ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት የስራ ሃላፊዎቹ፤ ከዚህ በፊት ግማሹ ነጋዴ እየከፈለ ቀሪው ሳይከፍል መቆየቱን ታሳቢ በማድረግ ሁሉንም ዜጋ በእኩል ለማገልገል ከሚል እሣቤ ሳይከፍሉ የቆዩት እንዲከፍሉ ማድረግ ተገቢ መሆኑን አመልክተው፤ የክፍያ አፈፃፀሙንና ሂደቱን በተመለከተ ከደንበኞች የሚቀርቡ ቅሬታዎች በአስተዳደራዊ እርምጃ የሚፈቱበት መፍትሔ አማራጭ መቀመጡን አስታውቀዋል፡፡ ከነዚህ አስተዳደራዊ እርምጃዎች መካከልም የተከማቸ ግብር ከሆነ ደንበኛው በረጅም ጊዜ እንዲከፈል እንዲሁም ቀደም ሲል ቅጣትና ወለድ መጨመር አለበት ተብሎ የነበረው ቀርቶ ያለባቸው እዳ ብቻ ተሰልቶ ከወለድና ቅጣት ነፃ በሆነ መልኩ እንዲከፍሉ የሚሉት ይገኙበታል፡፡

ከዚህ ባለፈ አንከፍልም ለሚሉት በህጉ አግባብ ባስልጣኑ እርምጃዎች ይወስዳል ብለዋል - ሃላፊዎቹ፡፡ የስራ ሃላፊዎቹ በሙስና ተጠርጥረው ስለተያዙት ከፍተኛ ባለስልጣናትና ባለሀብቶች እንዲሁም የተለያዩ ስራ ሃላፊዎች ጉዳዩ በፍርድ ቤት የተያዘ መሆኑን በመጥቀስ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡ በባለስልጣኑ የአመራር ቦታ አዳዲስ ሰዎች ሲሾሙ ለስራ ሂደቱ እንግዳ ስለሚሆኑ በአሰራሩ ላይ ችግር ሊፈጠር ይችላል ተብሎ ለቀረበው አስተያየትም፣ በፀረ ሙስና ኮሚሽን እርምጃው ከተወሰደ በኋላ ወደ መስሪያ ቤቱ የመጣ አዲስ የስራ ሃላፊ አለመኖሩን ያመለከቱት የስራ ሃላፊዎቹ፤ መንግስትም በቀድሞ ሃላፊዎች ምትክ ለመሾም ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በነጋዴዎች የተሰጡት አስተያየቶችም በቀጣይ ለሚሠሩት ስራዎች ግብአት ይሆናሉ ተብሏል፡፡ የስራ ሃላፊዎቹ በውይይቱ ሁለተኛ አጀንዳም በባለስልጣኑ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ 865 ከፍተኛ ግብር ከፋዮች መኖራቸውን ገልፀው፤ በ2005 ዓመት ከነዚህ ግብር ከፋዮች ይሰበሰባል ተብሎ ከታቀደው 35 ቢሊዮን ብር ውስጥ እስካሁን 28 ቢሊዮን ብር መሰብሰቡንና በቀጣይም እያንዳንዱ ግብር ከፋይ የሚጠበቅበትን ግብር በግንቦትና በሰኔ ወር ከፍሎ እንዲጨርስ አሳስበዋል፡፡

Published in ዜና

ምቀኞች ቢበዙልን እኮ ባለ3 ዲጂት እድገት እናስመዘግብ ነበር !

         አንዳንዴ የአባቶችን ተረትና ምሳሌ እንዲሁም ብሂል ዝም ብሎ ማጣጣል “ፌር” አይመስለኝም። አንዳንድ ቀለም የዘለቃቸው የጦቢያ ምሁሮችና ዘመናይ ነን ባዮች ግን እነዚህን ሥነ ቃሎች ለድህነታችንና ኋላ ቀርነታችን ሰበብ አድርገው ያቀርባሉ፡፡ አላወቁም እንጂ ጦቢያችን ከእነመንግስቷ ቆማ የምትሄደው በእነዚህ ወርቃማ አባባሎች እኮ ነው፡፡ እውነቱን ለመናገር---ከእነዚህ ምሁር ነን ባዮች እኮ የጥንቶቹ አባቶቻችን በብዙ ነገር ሺ ጊዜ ይበልጧቸዋል፡፡ እናም “ከመጠምጠም መማር ይቅደም” እላቸዋለሁ - የአባቶቻችንን ብሂሎች የሚተቹትን የጦቢያ ምሁሮች፡፡ ይሄን ግሳፄ የምሰነዝረው ግን ዝም ብዬ አይደለም፡፡

ብሂሎቹ ለጦቢያ የህልውና መሠረት መሆናቸውን ስለደረስኩበት ነው፡፡ ለዛሬ ልዩ ትኩረት አድርገን የምንፈትሸው ከጥንት የአባቶች አባባል ከወረስናቸው ሥነቃሎች መካከል “ምቀኛ አታሳጣኝ” የሚለውን ወርቃማ ብሂል ነው፡፡ እውነቴን ነው የምላችሁ --- የጦቢያችን ህልውና የተመሰረተው ሙሉ በሙሉ በእዚህ ብሂል ላይ ነው፡፡ ብታምኑኝም ባታምኑኝም “ምቀኛ አታሳጣኝ” የሚለው ሥነ ቃል ባይኖር ጦቢያችን አትኖርም ነበር፡፡ ጥናቴ እንደሚጠቁመው፤ የአበሻ ዘር ምቀኛ ያጣ ዕለት መኖር ያቆማል (አሳዛኝ ቢመስልም ሃቅ ነው!) በአጠቃላይ የዕድገታችን በሉት የስልጣኔያችን ወይም በኢህአዴግ ቋንቋ የህዳሴያችን መሰረቱ “ምቀኛ አታሳጣኝ” የሚለው መሪ ሥነ ቃል ነው፡፡ አበሻ ሲፀልይ “ምቀኛ አታሳጣኝ” ይላል ሲባል አልሰማችሁም? ቀልድ ከመሰላችሁ እንደኔ ተሸውዳችኋል፡፡ ፈፅሞ የማያጠራጥር ሃቅ መሆኑን እኔ ላረጋግጥላችሁ እችላለሁ - በመረጃም በማስረጃም፡፡ እንኳን ዜጐች ራሳቸው ፖለቲከኞችም ከዚህ ሌላ ፀሎት እንደሌላቸው በአሉባልታ ሳይሆን በሁነኛ መረጃ ደርሼበታለሁ፡፡

ለነገሩ “ምቀኛ አታሳጣኝ” የሚለው ብሂል የጦቢያ የህልውና መሰረት የሆነው በኢህአዴግ ዘመን አይደለም፡፡ ከጃንሆይ ዘመን ጀምሮ ነው ይላል - የጥናት ውጤቴ፡፡ እስቲ ማስረጃዎችን እየመዘዝን ሃቁን እንፈትሽ፡፡ ከዚያ በፊት ግን ሰሞኑን በኢቴቪ “ሰው ለሰው” በተሰኘው ዝነኛ ድራማ ላይ ከተሰጡ አስተያየቶች ግራ ያጋባኝን ላጋራችሁ (አስተያየቱ ሰውኛ አይመስልም እኮ!) እንደ መሰለኝ “ሰው ለሰው” ወደ ቀጣዩ ሲዝን የመሸጋገሪያ አስተያየቶችን እያስተናገደ ነው፡፡ ባለፈው ረቡዕ ዕለት አስተያየት ከሰጡት ተመልካቾች መካከል ይበልጥ ትኩረቴን የሳበው አንድ ታዋቂ ኮሜድያን ነበር፡፡ በነገራችሁ ላይ ይሄ ኮሜድያን ሰዓሊና የዱር እንስሳት መብት ተሟጋች (Activist) መሆኑንም የሰማሁ መሰለኝ - በEBS የ“ጆሲ ቶክ ሾው” ላይ፡፡ እናላችሁ --- ስለ “ሰው ለሰው” ድራማ በሰጠው አስተያየት ኮሜዲ የሚመስል ደረቅ ቀልድ ለመፍጠር ሞክሯል (ህይወትና ኮሜዲ ተደበላልቆበታል ልበል?!) መጀመርያ ላይ እንዲህ አለ፡- “ሰው ለሰውን የማየው ባገኘሁበት ቦታ ነው፤ ቴሌቪዥን በሌለበትም አያለሁ” (ኮሜዲም ከሆነ ቱርጁማን ያስፈልገዋል) ቀጥሎ ደግሞ “ሰው ለሰውን የማየው በዓይኔ ነው” አለና አረፈው (በአፍንጫው ሊያይ አስቦ ነበር?) ከዚያም ከድራማው መወገድ አለባቸው የምላቸው (የፀረ-አብዮት እርምጃ መሰለው እንዴ!) አለና የገፀባህርያቱን ስም ይዘረዝር ገባ፡፡

በመጨረሻም “ሁሉም ገፀ ባህርያት ቢወገዱ ፊልሙ የበለጠ አሪፍ ይሆናል” ብሎ ቅጥአምባሩ የጠፋ ነገር ተናግሮ ሄደ፡፡ እኔ የምላችሁ … ድንገት በብሔራዊ ቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ብሎ ዘባርቆ መሰወር ይቻላል እንዴ? ቤታችን ድረስ መጥቶ ግራ አጋብቶን እኮ ነው ላጥ ያለው፡፡ ምናልባት ሁሉ ነገሬ የተሰራው ከኮሜዲ ነው ሊለን አስቦ ይሆን? (ለዛሬ አልተሳካልህም ብለነዋል!) ከሁሉም የገረሙኝ ደግሞ “የሰው ለሰው” ፕሮዱዩሰሮች ናቸው፡፡ ይሄንን በፌዝ የተሞላ “ፉገራ” ያቀረቡት ምን ይፈይድልናል ብለው ነው? ምናልባት ሊያዝናኑን አስበው ይሆን? (እነሱም አልተሳካላቸውም!) አሁን በቀጥታ የምናመራው “ምቀኛ አታሳጣኝ” ወደሚለው የጦቢያችን የዘወትር ፀሎት ነው፡፡ በዚህ ወጋችን ይሄ ብሂል የቱን ያህል ከማህበራዊ፣ ባህላዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ህይወታችን ጋር በእጅጉ እንደተቆራኘ እንቃኛለን - ከሦስት መንግስታት አብነቶችን እየነቀስን፡፡ (ጥናቱ የንጉሱ፣ የደርግንና የኢህአዴግ መራሹን መንግስታት ያካትታል!) በሉ ከጃንሆይ ዘመን እንጀምር፡፡ በእጄ ላይ በገባው መረጃ መሰረት፤ ንጉሱ ትልቁን ጊዮን ሆቴል (ገዢ ያጣውን ማለቴ ነው!) እና ቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርትን አመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ አሰርተው ያጠናቀቁት “ምቀኛ አታሳጣኝ” በሚለው ብሂል ላይ ተመስርተው ነው፡፡ እንዴት ሆነ መሰላችሁ? የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መቀመጫውን በኢትዮጵያ እንዲያደርግ ሃሳብ ሲቀርብ ብዙ የአፍሪካ አገራት ተመቅኝተውን ነበር - እማኞች እንደሚናገሩት፡፡

ምቀኝነታቸው ግን በበቂ ምክንያት ላይ የተመሰረተ ነበር፡፡ ኢትዮጽያ በቂ ሆቴል እንደሌላት፣ አውሮፕላን ማረፍያ እንዳልገነባች፣ መንገድ እንዳልሰራችና ንፅህና እንደሚጐድላትም በዝርዝር አስረዱ። (ምቀኞቹ! ) ንጉሱና ሚኒስትሮቻቸው ይሄ ሁሉ ሃሰት መሆኑን ለማሳየት ነው በእልህና በቁርጠኝነት መትጋት የጀመሩት፡፡ ደግሞም ተሳካላቸው፡፡ በ9 ወር ውስጥ ጊዮን ሆቴል ተገነባ፡፡ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላንም ተሰራ፡፡ እኒያ ምቀኞች “ኩም” አሉ። የአፍሪካ አገራቱ ባይመቀኙንስ ኖሮ? ጊዮንም ኤርፖርትም መቼ እንደሚሰሩ ለማወቅ ይቸግራል፡፡ በነገራችሁ ላይ በአዲስ አበባ የቴሌቪዥን ስርጭት የተስፋፋውም ከዚሁ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ጋር ተያይዞ መሆኑን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ “ምቀኛ አታሳጣኝ” የሚለው ብሂላችን ቀላል ጠቀመን! ወታራዊው የደርግ መንግስት እንዲያ በጦርነት ውስጥ ተመስጐ እንኳ ከአፍሪካ ግዙፉን የጦር ሰራዊት የገነባው እንዴትና ለምን ይመስላችኋል? መቼም ለአፍሪካ ሰላምን ለማስፈን ብሎ እንዳልነበር ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ይልቁንም ከሶማሊያ ጀምሮ የጦቢያ ጥንካሬ የማያስደስታቸው የአፍሪካና የአረብ አገራት እንዳሉ ስለሚያውቅ ነው፡፡ እናም “ምቀኛ አታሳጠኝ” እያለ ራሱን በጦር ሃይል በደንብ አድርጐ አደረጀ (የማታ ማታ በኢህአዴግ ቢፈረካከስም!) ወደ ኢህአዴግ መራሹ መንግስትም ስንመጣ ነገሩ ተመሳሳይ ነው፡፡

ቀደም ሲል እንዳልኳችሁ ኢህአዴግም “ምቀኛ አታሳጣኝ” በሚል ፍልስፍናዊ ብሂል ነው የሚመራው (የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ፍልስፍናስ--እንዳትሉኝ) አሁን ለምሳሌ የኢትዮጵያን ህዝብ ከዳር እስከዳር አንቀሳቅሷል የተባለው የህዳሴ ግድብ ምቀኛ ባይኖርብን ይታሰብ ነበር? (የማይሆነውን!) ግብፆች- ኢትዮጵያ ለግድቡ ሥራ ከለጋሽ አገራት ብድር እንዳታገኝ ዘመቻ በመጀመራቸው እኮ ነው “መሃንዲሶቹ እኛው፣ ግንበኞቹ እኛው፣ የፋይናንስ ምንጮች እኛው---” ብለን ከኪሳችን አውጥተን ልንገነባ የተነሳነው። ለእልሃችንና ለቁርጠኝነታችን ሃይል የሆነን ምንድነው ከተባለ--- ያለ ምንም ጥርጥር የግብፆች ምቀኝነት ነው፡፡ እናላችሁ --- ግብፆቹ በዚያው ምቀኝነታቸው ቢቀጥሉልን በበለጠ ፍጥነት ግድቡን አጠናቀን ዓለምን ጉድ ያሰኘ የሪከርድ ባለቤት እንሆን ነበር (ጥቅሙ የጋራ ነው ብዬ እኮ ነው!) ሌላ የቅርብ ጊዜ መረጃም ልሰጣችሁ እችላለሁ። የቦሌ አዲሱ መንገድ በምን ያህል ፍጥነት ተሰርቶ እንደተጠናቀቀ ሳትታዘቡ አትቀሩም፡፡ (ኢህአዴግ አስማት የጀመረ የመሰላቸው አልጠፉም) ምናልባት የአፍሪካ ህብረት ምስረታ የ50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓል ባይኖር ኖሮ ስንት ዓመት እንደሚሟዘዝ መገመት ይቸግራል፡፡ አያችሁ ---ለበዓሉ ከመጡት መሪዎች መካከል የአፍሪካ ህብረት ከአዲስ አበባ ወደሌላ አፍሪካ አገር እንዲዛወር የሚሹ ምቀኞች እንዳሉ ኢህአዴግ “ነቄ” ነበር።

እናም ቻይናዎችን ከጉድ አውጡኝ ብሎ በጥቂት ወራት ውስጥ አስፋልቱን አስማት በሚመስል ፍጥነት አዘረጋው፡፡ አያችሁልኝ-- የምቀኛን ፓወር! ከማጂክ እኮ ይበልጣል! “ምቀኛ አታሳጠን” የጦቢያ የህልውና መሰረት ነው የምላችሁ ለዚህ እኮ ነው፡፡ በነገራችሁ ላይ በዚሁ የአፍሪካ ህብረት በዓል ላይ እንግዶቹ መጥተው እስኪሄዱ ድረስ ውሃና መብራት እንዳይጠፋ የተቻለው ሁሉ ጥረት ይደረጋል ተብለን እንደነበር ትዝ ይለኛል (አልተሳካም እንጂ!) እኛ እኮ እንዲህ ከተባልን 21 ዓመት ሊሞላን ምን ቀረን፡፡ ግን እድሜ ለምቀኛ! በአፍም ቢሆን ከስንት ዓመት በኋላ ቃል ተገባልን፡፡ እውነቴን ነው የምላችሁ--- ምቀኛ ባይኖረን ኖሮ ባለሁለት ዲጂት እድገት የለም ነበር፡፡ ምቀኛ ባይኖረን ኖሮ ቀለበት መንገድ አይኖርም ነበር። ምቀኛ ባይኖረን ኖሮ የግል ፕሬስ አይታሰብም ነበር (አሁንስ የታለ እንዳትሉኝ) ምቀኛ ባይኖር ኖሮ ምርጫ የሚባል ነገር አይኖርም ነበር (አሁንስ የታለ ብትሉኝ ጆሮ የለኝም) ብቻ --- ሁሉነገራችን የተቃኘው “ምቀኛ አታሳጣኝ” በሚል የአበሻ ብሂል ነው፡፡ ኢህአዴግ ብቻ ሳይሆን አንዳንድ የመንግስት መ/ቤቶችም በራቸውን ከርችመው ይከርሙና ምቀኛ ሲነሳባቸው መረጃ ለመስጠት ቁጭ ብድግ ይላሉ፡፡

ይሄ ብሂል የጦቢያ መንግስታት ፀሎት ብቻ ግን እንዳይመስላችሁ፡፡ የሰፊው የአበሻ ልጅ ፀሎት ነው (መንግስት እኮ ከህብረተሰቡ አብራክ ነው የወጣው!) አዲስ አበባ ላይ ድንገት የበቀሉ የሚመስሉት ባለመስተዋት ፎቆችም በምቀኛ አታሳጣኝ ብሂል የተሰሩ ይመስሉኛል (ጥናት ባላደርግም) የጦቢያ ነጋዴን ታውቁት የለ! ገንዘብ ከባንክ ተበድሮ የጓደኛው ዓይነት ባለስንት ሚሊዮን ብር አውቶሞቢል የሚገዛ ጀግና እኮ ነው! አንዳንድ ከውጭ አገር መጥተው የበጐ አድራጐት ድርጅት ወይም ደግሞ ቢዝነስ ያቋቋሙ ዳያስፖራ ኢትዮጵያውያን የሚሰጡትን ኢንተርቪው ታዝባችሁ ከሆነ አንድ ነገር ትረዳላችሁ፡፡ የሰሩትን ነገር የሰሩት ምቀኛን ኩም ለማድረግ መሆኑን፡፡ ምን ይላሉ መሰላችሁ? “ነጮቹ ኢትዮጵያ የሚለውን ስም ከድርቅና ከረሃብ ጋር ነው የሚያያይዙት። የአቅሜን በማበርከት ይሄን ክፉ ገጽታ ለመቀየር ነው ወደ አገሬ ተመልሼ ኢንቨስት ያደረግሁት…” ምቀኛ ባይኖር እኮ በጦቢያ ምድር እግሩን የሚያነሳ አይኖርም ነበር ማለት ነው፡፡ ለዚህ ነው የጥንት አባቶቻችንን ማመስገን አለብን የምለው፡፡ እነሱ “ምቀኛ አታሳጣን” የሚለውን ብሂል ባይፈጥሩልን ኖሮ ጦቢያ አትኖርም ነበር ማለት እኮ ነው፡፡ ጦቢያ ከሌለች ደግሞ የአበሻ ዘር የለም ማለት ነው፡፡ ይሄውላችሁ … እዚህች አገር ላይ ብዙ መልካም ነገሮች የሚሰሩት ለእኛ ተብለው ሳይሆን ምቀኞቻችንን ኩም ለማድረግ እንደሆነ የፖለቲካ በፈገግታ ጥናት ይጠቁማል፡፡ እንደውም አንድ ሃሳቤን የሚያጠናክርልኝ ማስረጃ ትዝ አለኝ፡፡

የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ ከአዲስ አበባ እንዲነሳ ምቀኝነት ቢጤ የተቀነቀነበት ጊዜ ትዝ አይላችሁም- በኢህአዴግ ዘመን፡፡ ያኔ በአፍሪካ ህብረት ስብሰባ ላይ (ነፍሳቸውን ይማረውና) የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር፣ ንጉሱንና መንጌን ለአፍሪካ ህብረት ባበረከቱት አስተዋጽኦ ሰማይ ላይ ሰቀሏቸው፡፡ ይሄ እንግዲህ በኢህአዴግ ታሪክ የቀድሞ መንግስታት በበጐ ሲነሱ ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑ ነው - “ምቀኛ አታሳጣኝ” የሚለው ብሂል ያለውን ፓወር እኔ አልነግራችሁም!! እናም ጦቢያ በሁሉም ዘርፍ መጠነሰፊ ዕድገት ማስመዝገብ ትችል ዘንድ ምቀኞች በብዛት ያስፈልጓታል ባይ ነኝ፡፡ የጦቢያ መንግስት፣ የጦቢያ ፓርቲዎች፣ የጦቢያ ነጋዴዎች፣ የጦቢያ ምሁሮች፣ የጦቢያ አርቲስቶች ወዘተ ሁሉም የሚንቀሳቀሱት “ምቀኛ አታሳጣኝ” በሚል ብሂል ነው፡፡ ቆይ ቆይ --- ሰሞኑን የተመረቀውን ድንቅ የስፖርት አካዳሚ አይታችሁልኛል? (ቱቱቱ…በሉበት) እኔማ ምን አልኩ መሰላችሁ… “ከየትኛው አቅጣጫ የተነሳ ምቀኛ ይሆን አካዳሚውን እንድንሰራ እልህ ውስጥ የከተተን?” በነገራችሁ ላይ በባህርዳር፣ በትግራይ፣ በአዋሳና በኦሮምያ ክልል ትልልቅ ስቴዲየሞች ተጀምረው በእንጥልጥል ቀርተዋል፡፡ እናላችሁ --- እነዚህን ስቴዲየሞች ለማስጨረስ እንደሌላው ጊዜ ቴሌቶን ይዘጋጅ የሚል ሃሳብ አላቀርብም፡፡ (አሁንማ ምስጢሩን ደርሼበታለሁ!) ስቴዲየሞቹን በፍጥነት ለማጠናቀቅ “ጠብደል” ያሉ ምቀኞች ብቻ ነው የምንፈልገው - ከአፍሪካ ወይም ከእስያ አሊያም ደግሞ ከምዕራብ አገራት!! ለአገራችን ዕድገት እንቅፋት ሆኗል የተባለውን ሙስናን ጠራርጐ ለማጥፋትም ብቸኛው መፍትሔ ምቀኛ መፈለግ ነው፡፡

አገራችን በሙስና መጠቃቷን የሚለፍፍ ምቀኛ ካገኘን፣ ከጦቢያ ምድር ሙስና ውልቅ ብሎ ይጠፋል - እንደኩፍኝ!! ሰብዓዊ መብት እንዲከበርም ከምቀኛ የተሻለ መፍትሔ የለንም (ቢያንስ ለጊዜው) ሂዩማን ራይትስ ዎች አንድ ጊዜ ደህና አድርጎ ቢያብጠለጥለን እኮ ከእንቅልፋችን እንነቃ ነበር - “ምቀኛ አታሳጣኝ” በሚል ብሂል። በየጊዜው እየተዳፈነ ለመጣው የፕሬስ ነፃነትም መፍትሔ ሌላ ሳይሆን አስተማማኝ ምቀኛ ነው። ይሄውላችሁ --- የአፍሪካ ህብረት አባል አገራት ጦቢያ የፕሬስና የተቃዋሚ ፓርቲዎች ነፃነት በቅጡ የሚከበርባት አገር አይደለችም የሚል የምቀኝነት ጉርጉርምታ ቢያሰሙ ሁሉነገር መስተካከሉ ምንም አያጠራጥርም፡፡ ኢህአዴግን የሚያነቃው ምቀኛ ነው ብያችሁ የለም! በነገራችሁ ላይ እኔም ይሄን አምድ የበለጠ ማራኪና ተነባቢ ለማድረግ ስላቀድኩ፣ ዕቅዴን ወደተግባር ለመለወጥ የሚያነሳሳኝ ደህና ምቀኛ በማፈላለግ ላይ ነኝ። “ምቀኛ አታሳጣኝ” እያልኩ የዛሬውን ወጌን ቋጨሁ!!

በምስክርነት ይቀርባሉ አምስቱ ባለሃብቶች ናቸው ተብሏል ከገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣናት ጋር በተያያዘ የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ምርመራ ካካሄደባቸው 125 ተጠርጣሪዎች መካከል በ58 ላይ ክስ ሲመሰርት 52ቱ ከክስ ነፃ ሆነው በምስክርነት እንዲቀርቡ ሊደረግ መሆኑን ምንጮች ገለፁ፡፡ በምስክርነት ለመቅረብ ተስማምተው ከክስ ነፃ ከሆኑት ምስክሮች መካከል አምስቱ ባለሃብቶች መሆናቸውና ሌሎቹ ደግሞ በገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን እንዲሁም በተጠርጣሪ ባለሃብቶች ድርጅቶች ውስጥ ተቀጥረው የሚሰሩ መሆናቸው ታውቋል፡፡

ከክስ ነፃ የሆኑት ምስክሮች ከሙስና ተጠርጣሪዎች ጋር ግንኙነት የነበራቸው ቢሆንም ተሳትፎአቸው በጅምር የቀረና ያልተፈፀመ መሆኑን የጠቆሙ ምንጮች፤ ለፀረሙስና ኮሚሽን ጥቆማ በመስጠት ለምርመራ ስራው አስተዋፅኦ ያደረጉ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ምስክሮቹን በቅርበት ስለሚያቋቸው ጉዳት ሊያደርሱባቸው ይችላሉ በሚል ማንነታቸው በሚስጥር እንደሚያዝ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ በተጠርጣሪዎቹ ላይ ምስክርነት ከመስጠትም በተጨማሪ ገና ያልተያዙ ተጠርጣሪዎችንና ማስረጃዎችን በእነዚህ ምስክሮች አማካኝነት ለማግኘት እየተሞከረ ነው ተብሏል፡፡

Published in ዜና

የምዝገባ መረጃዎቹ በጠ/ሚኒስትሩ ቢሮ የመረጃ ማጠራቀምያ ቋት ይገባሉ

የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ባወጣው አራት አይነት የመኖሪያ ቤቶች ምዝገባ፤ ህገወጥ መረጃዎችን ያቀረቡና በህገወጥ መንገድ የተመዘገቡ ወገኖች ላይ ጥብቅ እርምጃ እንደሚወሰድ ያስታወቀ ሲሆን፣ ህገወጦችን ለሚጠቁሙ ዜጐች 15 በመቶ ወሮታ የሚከፈልበት አሠራር ተግባራዊ እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ የቤቶች ልማት አስተዳደር ኤጀንሲ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ መሥፍን መንግስቱ ከትናንት በስቲያ ለመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች በሰጡት ማብራሪያ፤ ከፍተኛ የመኖሪያ ቤት ችግር በሚታይባት አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የተጀመረው ፕሮግራም ይህ አብዛኛውን ነዋሪ ተጠቃሚ ያደርጋል ተብሎ እንደሚታሰብ ገልፀዋል፡፡

የከተማዋ ነዋሪዎች በእኩልና ፍትሃዊ በሆነ መንገድ የቤት ችግራቸውን እንዲያቃልሉ ታስቦ በከፍተኛ ጥንቃቄ የቤት ፈላጊዎች ምዝገባው እንደሚካሄድ ጠቁመው፤ በህገወጥ መንገድ ለመመዝገብ በሚሞክሩና ከወጣው መስፈርት ውጪ ተመዝግበው በሚገኙ ዜጐች ላይ የማያዳግም ጥብቅ እርምጃም እንደሚወሰድ ተናግረዋል፡፡ እነዚህን ህገወጦች ለሚመለከተው አካል ለሚጠቁሙ ወገኖችም የ15% ወሮታ ለመክፈል የሚያስችል አሠራር ለማውጣት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አቶ መስፍን ጨምረው ገልፀዋል፡፡ ምዝገባው በከፍተኛ የቴክኖሎጂ መሣሪያዎች የሚከናወን መሆኑን የተናገሩት ሃላፊው፤ መረጃዎቹ በኔትወርክ እንዲያያዙና በጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ በሚገኝ የመረጃ ማጠራቀሚያ ቋት ውስጥ እንዲገቡ ለማድረግ የሚያስችል አሠራር መደራጀቱንም ገልፀዋል፡፡

መስተዳድሩ የመኖሪያ ቤት ፈላጊዎች የመመዝገቢያ ቀናትን ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ ቤት ፈላጊዎች በተሰጠው የጊዜ ገደብ ብቻ ቀርበው እንዲመዘገቡ አሳስቧል፡፡ በወጣው ፕሮግራም የ10/90 እና 20/80 ወይም የኮንዶሚኒየም ቤቶች ተመዝጋቢዎች ከሰኔ 3 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ሰኔ 21 ቀን 2005 ዓ.ም ድረስ ምዝገባቸውን የሚያካሂዱ ሲሆን፣ በ1997 ዓ.ም ተካሂዶ በነበረው የኮንዶሚኒየም ቤቶች ምዝገባ ተመዝግበው እስከ አሁን ድረስ እጣው ያልወጣላቸው ዜጐች በዚህ ምዝገባ እንደ አዲስ ሊመዘገቡ እንደሚገባም ተገልጿል፡፡ የቀድሞ የኮንዶሚኒየም ምዝገባ በአዲሱ ምዝገባ ተሻሽሎ የሚከናወን ሲሆን ከዚህ በኋላ የ1997 ዓ.ም ምዝገባ ዋጋ እንደማይኖረው ተጠቁሟል፡፡

ቤት ፈላጊዎች ከተመዘገቡ በኋላ በድጋሚ በሚካሄደው የማጣሪያ ምዝገባ የጣት አሻራ እንዲሰጡ እንደሚደረግና ለዚህም የሚያገለግሉ የመሣሪያዎች ግዢ እየተከናወነ እንደሆነ ዋ ሥራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡ ተመዝጋቢዎች እንደየሚመዘገቡበት የቤት ልማት ዓይነት መቆጠብ የሚገባቸውን የገንዘብ መጠን በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ብቻ በመቆጠብ የባንክ ደብተር መያዝ ይኖርባቸዋል፡፡ ነባር የኮንዶሚኒየም ተመዝጋቢዎች፣ በአዲሱ ምዝገባ ለባለ ሶስት መኝታ ቤት 685 ብር፣ ለባለ ሁለት መኝታ ቤት 561 ብር፣ ለባለ አንድ መኝታ ቤት 274 ብር እንዲሁም ለስቱዲዮ 151 ብር በቅድሚያ ሊቆጥቡ እንደሚገባ ተገልጿል፡፡ ለአዲሱ የ20/80 ወይም የኮንዶሚኒየም ቤቶች ምዝገባ ለባለ ሶስት መኝታ ቤት 489 ብር፣ ለባለ ሁለት 401 ብር እንዲሁም ለባለ አንድ 196 ብር መቆጠብ ያስፈልጋል፡፡ በቀድሞ የኮንዶሚኒየም ቤቶች ምዝገባ ተመዝግበው እጣ ያልወጣላቸውና በዚህ ምዝገባ እንደ አዲስ የሚመዘገቡ ነባር ተመዝጋቢዎች ከአዲሶቹ ቅድሚያ ተሰጥቷቸው እንደሚስተናገዱም ተገልጿል፡፡

ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው ወገኖች የተዘጋጀው የ10/90 የስቱዲዮ ቤቶች ደግሞ 187 ብር በቅድሚያ መቆጠብ የሚገባ ሲሆን፣ የእነዚህ ቤቶች ግንባታ በአብዛኛው እየተጠናቀቀ እንደሆነም ተጠቁሟል፡፡ የ40/60 ቤቶች ምዝገባ ተጠቃሚ የሚሆኑት የተሻለ ገቢ ያላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች አካላት እንደሆኑ የተናገሩት አቶ መስፍን፤ ሙሉ ክፍያ ለሚከፍሉ ተመዝጋቢዎች ቅደሚያ እንደሚሰጥም ጠቁመዋል፡፡ የእነዚህን ቤቶች ምዝገባ በተመለከተ በባንክ በኩል መመሪያዎች ወጥተው ተፈፃሚ እንደሚደረጉም ሃላፊው ገልፀዋል፡፡ የማህበራት ምዝገባም በቡድን እየተደራጁ በሚመጡ ወገኖች ተግባራዊ እንደሚደረግ ጠቁመው፤ በምዝገባ ወቅት የቤቱ ዋጋ 50% እና መሬት ተዘጋጅቶ የግንባታ ፈቃድ ከመሰጠቱ በፊት 50% በዝግ ሂሳብ የሚቀመጥ እንደሚሆን ተገልጿል፡፡ ለ40/60 ቤቶች ምዝገባው ከነሐሴ 6 እስከ ነሐሴ 17 ቀን 2005 ዓ.ም ድረስ የሚከናወን ሲሆን ማህበራት ደግሞ ከሐምሌ 15 ቀን እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2005 ዓ.ም ድረስ ምዝገባቸውን እንደሚያከናውኑ ተጠቁሟል፡፡ በአዲሱ የቤት ፈላጊዎች ምዝገባ በቀን ከ100ሺ በላይ ሰዎች ይመዘገባሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም አቶ መስፍን ተናግረዋል፡፡ የመንግስት ሠራተኞችን በተመለከተ በልዩ የምዝገባ አሠራር በየመ/ቤቶቻቸው በኩል እንዲከናወን መወሰኑም ተገልጿል፡፡

Published in ዜና

በወር 140 ሚ. ሞባይል ስልኮች ተሽጠዋል - ግማሾቹ (70 ሚ) እንደ አይፎንና ጋላግክሲ የመሳሰሉ ‘ስማርትፎን’ ናቸው። በስማርትፎን ሽያጭ ዘንድሮ መሪነቱን ከአፕል የተረከበው ሳምሰንግ፣ ከጋላክሲ ሞባይሎች ሽያጭ በየወሩ በአማካይ 8 ቢ. ዶላር ገደማ ገቢ እያገኘ ነው። የአፕልም ገቢ ተቀራራቢ ነው፤ ወደ ስምንት ቢ. ዶላር የሚጠጋ ገቢ ከአይፎን ሞባይሎቹ ሽያጭ በማስገባት በሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የሳምሰንግ ሩጫ የሳምሰንግ ስኬት ይበልጥ እያደገ እንደሚሄድ በእርግጠኛነት የሚገልፁ ዘገባዎች ምክንያታቸውን ሲያስረዱ፣ አዲሱ ‘ጋላግሲ ኤስ4’ ከፍተኛ ተወዳጅነት ማግኘቱን ይጠቅሳሉ። በእርግጥ ነባሩ ጋላግክሲ ኤስ3 ሞባይልም፣ ዋነኛ የአይፎን ተቀናቃኝ ለመሆን በመቻሉ፣ ሳምሰንግ በሞባይል ምርት የመሪነቱን ደረጃ እንዲቆናጠጥ ረድቶታል።

ከወር በፊት ለገበያ የቀረበው ኤስ4 ግን፣ ገና ካሁኑ ሪከርድ ሰብሯል። ኤስ3 ለገበያ የቀረበ ጊዜ፣ አስር ሚሊዮን ሞባይሎችን ለመሸጥ ሁለት ወራት ፈጅቶበት ነበር። ኤስ4 ግን በአንድ ወር ውስጥ ነው አስር ሚሊዮን የተቸበቸበው። በሽያጭ መጠን መሪነቱን መያዝ ግን፣ በአትራፊነትም አንደኛ መሆን ማለት አይደለም። ሳምሰን በየወሩ ከ2 ቢ. ዶላር በላይ ትርፍ እያገኘ እንደሆነ የገለፁ የሰሞኑ ዘገባዎች፣ አፕል በየወሩ የሚያገኘው ትርፍ ከ3 ቢ. ዶላር በላይ እንደሆነ ጠቅሰዋል። የሳምሰንግና የአፕል ኩባንያዎች ስኬት፣ ወደፊትም እያደገ እንደሚሄድ ይጠበቃል - የስማርትፎኖች ገበያ እየተስፋፋ ነውና።

ከመደበኛ ሞባይል ወደ ስማርትፎን ላለፉት አምስት አመታት በአይፎን መሪነት በፍጥነት እያደገ የመጣው የስማርትፎን ገበያ፣ ዘንድሮ ከሌላው መደበኛ ሞባይል ጋር በቁጥር ለመስተካከል እንደበቃ ጋርተር የተሰኘ የጥናት ተቋም ገልጿል። ካለፈው የጥር ወር ወዲህ፣ በመላው አለም በየወሩ 140 ሚ. ገደማ ሞባይሎች ለተጠቃሚ እንደተሸጡ ጋርተር ጠቅሶ፣ ከእነዚህም መካከል ሰባ ሚ. ያህሉ መደበኛ ሞባይሎች ሲሆኑ ሰባ ሚ. ያህሉ ደግሞ ስማርትፎን ናቸው ብሏል። በመደበኛ ሞባይልና በስማርትፎን ገበያ፣ በጥቅሉ ሳምሰንግ በየወሩ 35 ሚ. ገደማ ሞባይሎችን ሲሸጥ፣ ከመሪነት የወረደው ኖኪያ በወር 21 ሚ. ሞባይሎችን ሸጧል። አፕል 13ሚ.፣ ኤልጂ 5ሚ.፣ ከቀድሞ ቦታው አንድ ደረጃ የወረደው ዜድቲኢ ከ4.5 ሚ በላይ፣ ደረጃውን እያሻሻለ የመጣው ሁዋዌ ደግሞ ወደ 4 ሚ. ገደማ ሞባይሎችን ለገበያተኛ አድርሰዋል። የኩባንያዎቹ ስኬታማነት የሚለካው ግን በጥቅል የሞባይል ሽያጭ ሳይሆን በስማርትፎን ሽያጭ ነው - ስማርትፎን ከፍተኛ ገቢ ያስገኛልና። የስማርትፎን ፉክክር በስማትፎን ገበያውን የሚመሩት፣ የጋላክሲ አምራቹ ሳምሰንግ እና የአይፎን አምራቹ አፕል ናቸው። ሳምሰንግ፣ የጋላግሲ ኤስ ሞባይል ምርቱን ባለፈው አመት በሃምሳ በመቶ በማሳደግ፣ አሁን በየወሩ 23 ሚ. ገደማ ሞባይሎችን እየሸጠ መሆኑን ጋርተር ገልጿል።

አፕልም እንዲሁ፣ ምርቱን በማስፋት በየወሩ 13 ሚ. አይፎኖችን ለተጠቃሚዎች ሸጧል። የስማርትፎን ምርታቸውን በእጥፍ ያሳደጉት ኤልጂ እና ሁዋዌ ብርቱ ተፎካካሪ ለመሆን የተዘጋጁ ይመስላሉ። ኤልጂ በወር ከ3 ሚ. በላይ፣ ሁዋዌ ደግሞ ወደ 3 ሚ. የሚጠጉ ሞባይሎችን ገበያ ላይ እያዋሉ ነው። በየእለቱ የሚሰራጩ መረጃዎችና ዘገባዎች ሲታዩ፣ የስማርትፎን ውድድር እየበረታ እንደሚሄድ ያመለክታሉ። የካናዳው ብላክቤሪ እና የታይዋኑ ኤችቲሲ፣ በያዝነው ወር የስማርትፎን ምርቶቻቸውን ለገበያ በማቅረብ የአለምን ትኩረት ስበዋል። ኖኪያና ሶኒም እንዲሁ በአዳዲስ ምርቶች ገበያውን ለመጋራት እየጣሩ ነው። ከዚህም በተጨማሪ፣ በቅናሽ ዋጋ ስማርትፎን የሚያመርቱ ኩባንያዎች ከየአገሩ ወደ ፉክክሩ መግባት ጀምረዋል። ሳምሰንግና አፕል፣ ለዚህ ውድድር ተዘጋጅተዋል። ሳምሰንግ ሰሞኑን ይፋ እንዳደረገው፣ ከጋላክሲ ኤስ4 በዋጋ ግማሽ ያህል የሚቀንስ ሚኒ ኤስ4 ለገበያ አዘጋጅቷል። አፕልም እንዲሁ፣ ሚኒ አይፎን5 ያመርታል ተብሎ ይጠበቃል።

ከህዝብ ቁጥር ጋር የሚስተካከል ሞባይል በመላው አለም በአጠቃላይ ወደ 7 ቢሊዮን የሚጠጉ የሞባይል ስልክ መስመሮች አገልግሎት ላይ ውለዋል። በአፍሪካም 550 ሚ. ያህል ሞባይሎች ለተጠቃሚዎች ደርሰዋል - በአማካይ ለሶስት ሰዎች ሁለት ሞባይል እንደማለት ነው (64%)። የኢትዮጵያ፣ ገና የዚህን ግማሽ ያህል እንኳን አልደረሰም። በየአመቱ 1.7 ቢሊዮን ያህል ሞባይሎች ለገበያ እንደሚቀርቡ የገለፀው ጋርተር፣ የስማርትፎን ድርሻ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየሰፋ ዘንድሮ ከ800ሺ በላይ እንደሚደርስ ጠቁሟል። ግማሽ ሞባይል፣ ግማሽ ላፕቶፕ (ታብሌት) ሳምሰንግ በስማርትፎን ሽያጭ ገበያውን መምራት ቢጀምርም፣ በ‘ታብሌት’ ገበያ ግን የአፕል አይፓድ አልተቻለም። አፕል፤ በወር ውስጥ ወደ ከ6 ሚ. ላይ አይፓዶችን በመሸጥ የአምናውን ሪከርድ ሰብሯል። ሳምሰንግ ወደ 3 ሚ. ገደማ እየሸጠ ይገኛል።

Published in ዜና