በ8ኛው የቢግ ብራዘር አፍሪካ ሪያሊቲ ሾው ከሚሳተፉት 28 ተወዳዳሪዎች ሁለት ኢትዮጵያውያን እንደሚገኙበት ታወቀ፡፡ ሁለቱ ኢትዮጵያውያን የ26 ዓመቷ መምህር እና የአዲስ አበባ ነዋሪ የሆነችው ቤቲ እና በደቡብ አፍሪካ ነዋሪና ተማሪ የሆነው የ23 ዓመቱ ቢምፕ ናቸው፡፡ መላው አፍሪካ በቀጥታ ስርጭት በሚያየው ውድድር በመሳተፌ ልዕልት አድርጎኛል ያለችው ቤቲ በውድድሩ ካሸነፈች በሽልማት ገንዘቡ የትራቭል ኤጀንሲ ማቋቋም እፈልጋለሁ ብላለች፡፡ በቢግ ብራዘር አፍሪካ ላይ በመሳተፍ የማገኘው ልምድ አጓጉቶኛል ያለው ቢምፕ በበኩሉ ፤ ውድድሩ ሃገሩን ለማስጠራት የሚችልበት መልካም አጋጣሚ እንደሆነ ገልፆ፤ ማሸነፍ ከቻለ በአዲስ አበባ የመዝናኛ ክለብ የመክፈት ሃሳብ እንዳለው ተናግሯል፡፡ ከመምህርነት ሙያዋ ባሻገር በአስተርጓሚነት የምትሰራው ቤቲ በቢግ ብራዘር አፍሪካ ኢፊሴላዊ ድረገፅ እራሷንነ ስትገልፅ ብልህ፤ በራስ መተማመን ያላት፤ ወሳኝ ሁኔታዎች በቁርጠኝነት የምጋፈጥ ነኝ ብላለች፡፡

ቀጠሮ አክባሪ፤ ምክንያታዊ እና ብዙ የሚያወሩ ሰዎችን እንደምትጠላ የምታሳውቀው ቤቲ መፅሃፍ የማነበብ ዝንባሌ እንዳላት አመልክታ ከሁሉ ማንበብ የምትወደው የግል ማስታወሻዋን እንደሆነ ገልፃለች፡፡ አፍሪካውያን ማንኛውንም ነገር ማሳካት እንደሚችሉ ለዓለም ህዝብ ያሳዩ ህዝቦች ናቸው የምትለው ቤቲ በደብረዝይት ያለው ኩሪፍቱ ሪዞርት ተወዳጅ መዝናኛዋ እንደሆነ ገልፃ የዓለም ሙዚቃ እና ፊልም ወዳጅ በመሆኗ ሆሊውድን ለማየት ሁሌም ያጓጓኛል ብላለች፡፡ ትውልዱ በአዲስ አበባ ቢሆንም አሁን በሚማርበት ደቡብ አፍሪካ የሚኖረው ቢምፕ በበኩሉ ራሱን ታማኝ፤ ግልፅ፤ አስተማማኝ እና ሃላፊነት ተቀባይ አድርጎ ይገልፃል፡፡ አፍሪካውያን ጓደኞች እንግዳ ተቀባዮች እና ብዙ አስደናቂ የባህል መስቦች ያሏቸው ህዝቦች ናቸው የሚለው ቢምፕ በቢግ ብራዘርስ ላይ በመካፈል በቲቪ መታየቱን መላው ቤተሰቡ ስለወደደለት ደስ ብሎኛል ብሏል፡፡

በገጣሚና ጋዜጠኛ በረከት በላይነህ የተፃፈው “የመንፈስ ከፍታ” የተሰኘ የግጥም መድበል ሰኞ በ11፡30 በዋቢሸበሌ ሆቴል ይመረቃል፡፡ በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች የተከፋፈለው “የመንፈስ ከፍታ”፡ የገጣሚው 48 ያህል ወጥ ግጥሞችና፣ ጃላላዲን ሩሚን ጨምሮ ሌሎች የታወቁ የፋርስ ገጣሚያን የፃፏቸው 31 ትርጉም ግጥሞች ተካተውበታል፡፡ በምረቃ ስነስርአቱ ላይ ታዋቂ ወጣትና አንጋፋ ገጣሚያን ስራዎቻቸውን ያቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የመጽሐፉ ዋጋ 30 ብር ነው፡፡ ገጣሚው በቅርቡም “ንፋስ አፍቃሪዎች” የተሰኘ የግጥም ሲዲ አሳትሞ ለገበያ ለማቅረብ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡

በየሁለት ሳምንቱ በመፃሕፍት ላይ የንባብ እና የውይይት መድረክ በማድረግ የሚታወቀው ሚዩዚክ ሜይ ዴይ የመወያያ ሥፍራውን ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም ሬዲዮ ፋና አካባቢ ወደሚገኘው ብሔራዊ ቤተመፃሕፍትና ቤተመዛግብት ድርጅት (ወመዘክር) አዛወረ፡፡ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተመፃሕፍትና ቤተመዛግብት አዳራሽ ለውይይት የሚቀርበው መጽሐፍ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ በ1993 ዓ.ም ያሳተመው የኮሌጅ ቀን ግጥሞች” የተሰኘ የግጥም መድበል እንደሆነ ታውቋል፡፡

በመጽሐፉ ከተሰነዱት ግጥሞች መካከል የኃይሉ ገብረዮሐንስ (ገሞራው) “በረከተ መርገም” እና የዮሐንስ አድማሱ “እስቲ ተጠየቁ” ይገኙበታል፡፡ መነሻ ሃሳብ በማቅረብ ለሶስት ሰዓታት የሚዘልቀውን ውይይት የመሻ ሃሳብ በማቅረብ የሚመሩት የሥነጽሑፍ ባለሙያው የዶክትሬት ዲግሪ ተማሪ ገዛኸኝ ፀጋው ናቸው፡፡

የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ቢል ክሊንተን ከዋይት ሃውስ ከወጡ ወዲህ ባለፉት 12 አመታት በተለያዩ ቦታዎች ንግግር በማቅረብ ብቻ 106 ሚሊዮን ዶላር ማግኘታቸው ሲኤንኤን ዘገበ፡፡ ቢል ክሊንተን በአንድ መድረክ ንግግር ለማቅረብ በአማካይ 200ሺ ዶላር ይከፈላቸዋል፡፡ የቀድሞው ፕሬዝዳንት በንግግር አዋቂነታቸው በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ተፈላጊ ናቸው፡፡ በናይጄርያ ሌጎስ በአንድ መድረክ የተከፈላቸው 700ሺ ዶላር በተመሳሳይ የስራ ድርሻ የተገኘ ትልቁ ክፍያ እንደሆነ ታውቋል፡፡

ቢል ክሊንተን በንግግር አዋቂነታቸው አምና ከፍተኛ ተፈላጊነት እንደነበራቸው የሚገልፀው ሲኤንኤን በመላው ዓለም በ73 መድረኮች በመስራት 17 ሚሊዮን ዶላር እንደተከፈላቸው ገልጿል። ቢሊ ክሊንተን 42ኛው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት የነበሩ ናቸው፡፡ በበጎ አድራጊነት፤ በንግግር አዋቂነት ፤ በዴሞክራት ፖለቲከኛነት እና በጥብቅና ሙያቸው ከፕሬዝዳንትነት ከወረዱ በኋላ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያላቸው ቢል ክሊንተን 80 ሚሊዮን ዶላር ሃብት እንዳላቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡

ከኤሌክትሮኒክስ ሙዚቃ ዲጄዎች፣ ሆላንዳዊ ዲጄ ቲዬስቶ 75 ሚሊዮን ዶላር መሪነቱን እንደያዘ ሴለብሪቲ ኔትዎርዝ ገለፀ። ለግሉ በገዛው ጄት አውሮፕላን በመላው ዓለም በመዘዋወር የሚሰራው የ44 ዓመቱ ዲጄ ቲዬስቶ፣ በአማካይ ለአንድ ምሽት ስራ እስከ 250ሺ ዶላር እየተከፈለው ባለፈው ዓመት ብቻ ሃያ ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝቷል። ቲዮስቶ፣ በሙዚቃ መሸጫ ሱቅ እየሰራና ፒዛ እየተላላከ ይኖር እንደነበር አስታውሶ፣ ዲጄነትን የጀመረ ጊዜ ባንድ ምሽት ሃምሳ ዶላር ብቻ ይከፈለው እንደነበር ገልጿል።

ከዲጄነት ጎን ለጎን፣ እንደ ሌሎቹ ዲጄዎች በሙዚቃ ፕሮዲውሰርነትና በአቀናባሪነት እየሰራ አምስት ሙሉ አልበሞችን እና ሶስት የሪሚክስ አልበሞችን ለገበያ አብቅቷል፡፡ ባንድ ምሽት በአማካይ ከ100ሺ እስከ 500ሺ ዶላር ከሚከፈላቸው ታዋቂ የኤሌክትሮኒክስ ሙዚቃ ዲጄዎች መካከል አንዳንዶቹ፣ የግል ጄት አውሮፕላንና ውድ ቪላ እየገዙ ለቅንጦት ኑሮ ገንዘባቸውን ሲያፈሱ ይታያሉ። ሴሌብሪቲ ኔትዎርዝ ባወጣው የዲጄዎች ደረጃ፣ ከሁለተኛ እስከ አምስተኛ የወጡት ከሃምሳ እስከ ስድሳ ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ሃብት ያላቸው ዲጄዎች ናቸው።

እናት ህፃን ልጇን አዝላ ከገበያ እየተመለሰች ነው፡፡ በዘንቢሏም እቤት ለሚጠብቋት ልጆቿ የሚሆን ሙዝ፣ ሸንኮራ አገዳና መሰል ቁሶች ይዛለች፡፡ የእናታቸውን ከገበያ መመለስ የተመለከቱ ህፃናት ልጆቿና ውሻቸው እናቲቱን ለመቀበል ወደ እሷ ሲሮጡ የሚያሳየው ሥዕል ዓይንን ጨምድዶ የሚይዝ ቅርፅ ነው፡፡ የግርማችን ፒ ኤል ሲ ሥራ አስኪያጅና የአክሲዮኑ አባል አቶ አንዷለም ግርማ “ከሁሉ በላይ ይኼ ምሥል ልቤን ይገዛዋል፡፡ ይህ ነገር የእኔም፣ የአንቺም የሁሉም ሰው እውነተኛ የህይወት ነፀብራቅ ነው” ይላሉ፡፡ ገበያ ሄዳ ሸንኮራና ሙዝ ለልጇ ይዛ ያልመጣች እናት አለች ብለው እንደማያምኑም አጫውተውኛል፡፡ ሌሎች ሥዕሎችም በብዛት ይታያሉ፡፡ በህንፃው ስር ባለው ሰፊ በር ወደ ውስጥ ሲዘልቁ ነው የቤቱን ተዓምራት መመልከት የሚጀምሩት፡፡ ገና ሲገቡ መሬት ላይ ባለው ሰፊ ባር መሀል ላይ ትልቋና ባለ ግርማ ሞገሷ ንስር፣ ክንፏን ዘርግታ ምንቃሯን ከፈት አድርጋ ይመለከታሉ፡፡

እሱን አይተው ሳይጠግቡ ንስሯ በተቀረፀችበት ፏፏቴ ዙሪያ የተደረደሩት የዝሆን ምስል ያላቸው ወንበሮች እንደገና ያስገርምዎታል፣ እዛው ላይ ቆመው ዞር ዞር እያሉ ግድግዳውን መቃኘት ሲጀምሩ ደግሞ “ለመሆኑ ይኼ ቤት ሆቴል ነው ወይስ ሙዚየም” ብለው እንደሚጠይቁ ጥርጥር የለኝም፡፡ በግድግዳው ላይ ተቀርፀው በልዩ የቀለም ህብር ካማሩ ሥዕሎች ውስጥ ፍቅር፣ ጭፈራ፣ የአባ ገዳ ሥርዓት፣ የእርቅ ሥርዓት፣ የፈረስ ግልቢያ፣ የክሊዮፓትራ ምስል፣ የገጠሩ ሕዝብ አኗናር…በስዕልና በቅርጽ ያልተዳሠሠ ነገር የለም፡፡ ይህን ትንግርት የሚመለከቱት በአዳማ ከተማ መብራት ኃይል ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ቀበሌ 06 ሞቅ ደመቅ ካሉት የምሽት ጭፈራ ቤቶች በአንዱ ነው፡፡ ታዲያ ለሥራም ይሁን ለመዝናናት ወደ ከተማዋ ጐራ ያለ ማንኛውም ሰው፣ አካባቢውን ሳይጐበኝ ይመለሳል ለማለት ይቸግራል፡፡ አንዳንዶች አካባቢውን “የአዳማው ቺቺኒያ” ይሉታል፡፡

በዚሁ አካባቢ ግን አንድ ትልቅ ኤግል ተፈጥሯል፡፡ ኤግሉ ከዚህም በፊት የነበረና ገበያ የነበረው ሆቴል ሲሆን ወደ ትልቅ ኤግልነት ለመቀየር አራት አመት ፈጅቷል፡፡ ተጠናቆ ስራ ከጀመረም ገና ሦስት ወሩ ነው፡፡ የቤተሠቡ ጊዜና ጉልበት ሳይታሠብ 55 ሚሊዮን ብር የጨረሠው አዲሱ ኤግል፣ 40 የመኝታ ክፍሎችን የያዘ ባለ ሰባት ፎቅ ህንፃ ነው፡፡ ኤግል ሆቴል በአምስት ወንድማማቾች፣ በእህትና በእናታቸው በወ/ሮ አበበች ወ/ሥላሴ የተመሠረተ አክሲዮን ነው፡፡ የቤተሰቡ መነሻ አርሲ ውስጥ በአርባ ጉጉ አውራጃ ጮሌ በተባለች መንደር ውስጥ ሲሆን አባታቸው አቶ ግርማ ኃይሉና ባለቤታቸው ወ/ሮ አበበች ወ/ሥላሴ የቢዝነስ መሠረታቸው ሆቴል እንደሆነ የአክሲዮኑ ሥራ አስኪያጅ አቶ አንዷለም ግርማ ይናገራሉ፡፡

ልጆቻቸውን በፍቅርና በስራ ገርተው ያሣደጉ ጠንካራ ወላጆች እንደነበሩ የሚናገሩት አቶ አንዷለም፤ ታላላቆቻቸውም ሆነ ታናናሾቻቸው ከልጅነት ጀምሮ ደረጃ በደረጃ ሥራን ከቤተሠብ ጋር እየለመዱ እየተዋደዱና እየተከባበሩ ማደጋቸውን ይገልፃሉ፡፡ “ለምሣሌ እኔን ብትወስጂ አርሲ በነበረን ሆቴልና ሥጋ ቤት ውስጥ ለሰው ስጋ በማድረስ፣ ከዚያ ለቆራጭ በማቀበል ብሎም ሥጋ ቆራጭ በመሆን ደረጃ በደረጃ ሠርቻለሁ” በማለት የስራ ተሞክሯቸውን አጫውተውኛል፡፡ “የቤተሰቡ ትልቁ የትምህርት ደረጃ 12ኛ ክፍልን ማጠናቀቅ ነው፣ ከዚያ በላይ የተማረ የለም” ያሉት አቶ አንዷለም ፤ ከሰባት ዓመት ዕድሜያቸው ጀምሮ አዳማ ውስጥ እንዳደጉ ይናገራሉ፡፡ ትልቁ ኤግል ከመሠራቱ በፊት ከኪራይ ቤቶች የተከራዩት ትንሽ ሆቴል እንደነበር ገልፀው፤ ትንሹም ሆቴል በጣም ደማቅና የከተማዋን ሁኔታ ያገናዘበ እንደነበር ያብራራሉ፡፡ “ሆቴሏ በጣም ብዙ ገበያና ጥቅም የምታስገኝ ነበረች” የሚሉት የፒኤልሲው ስራ አስኪያጅ፤ በቤተሠቡ ውስጥ ያለው ትልቅ ነገርን መስራት እንደሚቻል የማመን ብቃት አሁን ትልቁን ኤግልና በውስጡ የዓይን ማረፊያ የሆነውን የባህል የፍቅር፣ በአጠቃላይ የጥበብ ሥራ መፍጠሩን ገልፀው፤ ወረቀት ላይ ያሠፈሩት ቅርፅና ሥዕል በቤተሰባችን አዕምሮ ውስጥ ተቀርፆ ያለቀውን ነው” ይላሉ አቶ አንዷለም፡፡

የተዋበ ሆቴል ለመሥራት የነበራቸውን ፍላጎት ሲናገሩ “ሰው በመጠጥና በምግብ ሰውነቱን ከመሙላት ባለፈ አዕምሮውም ምግብና እረፍት እንደሚያስፈልገው በማመን ነው የሠራነው” የሚሉት ሥራ አስኪያጁ፤ ይኼ ሲሠራ ግን ቀጥታ ዒላማው ገንዘብ ያመጣል የሚል ሳይሆን ሰዎች የበለጠ ምቾት እንዲሰማቸው ማድረግ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ወደ ሆቴሉ ቅኝት ስንመለስ ፏፏቴው ሲለቀቅ የተለያዩ ትዕይንቶች ይታያሉ፡፡ ለምሳሌ ኤግሏ የተቀረፀችው ወፎች ውሃ ሲነካቸው ለማራገፍ ክንፋቸውን በሚዘረጉበት ዓይነት ነው፡፡ ከሁሉም ያስገረመኝ ቅርፅ ደግሞ እነሆ፡- አንዲት እንቁራሪትና አንድ ህፃን ፊት ለፊት ተፋጠው ተቀምጠዋል፡፡ ፏፏቴው ሲለቀቅ እንቁራሪቷ ህፃኑ ላይ ትተፋለች፤ ህፃኑ ደንግጦ ሲያያት የሚያሳይ ቅርፅ ነው፡፡ ነገሩ ለህፃናት መዝናኛነት ታስቦ ቢሠራም ትልልቆችንም የሚያፈዝ ነው፡፡ ሁለቱን ፎቅ ወጥተው ቴራሱ ላይ ሲደርሱ እንደ ፔንዱለም ወዲህ ወዲያ የሚወዛወዝ ወንበር ያገኛሉ፡፡ ይህ ወንበር መኻል ላይ ጠረጴዛ ያለውና ፊት ለፊት ለሚቀመጡ ሰዎች በተለይም ህፃናት እየተወዛወዙ እንዲዝናኑ የታሰበ ቢሆንም በወንበሩ እየተወዛወዙ ሲዝናኑ ያየናቸው ግን አዋቂዎች ናቸው፡፡ አጠቃላይ የሆቴሉ አሠራር የአምፊ ቴአትር (ጣሪያ የሌለው) አይነት ነው ፤ለምሣሌ ቴራስ ላይ ቁጭ ብለው አቆልቁለው፣ አሊያም አግድመው በየፎቆቹ ላይ ያሉትን ትዕይንቶች በግልፅ ለመመልከት ምቹ ነው፡፡ በሆቴሉ የተለያዩ ግድግዳዎች ላይ በፈረንሳይኛ፣ በጀርመንኛና በቻይንኛ ቋንቋ ኤግል ሆቴል የሚሉ ፅሁፎች ተፅፈዋል፡፡

አቶ አንዷለም ስለዚሁ ሲያስረዱ፤ ትንሿ ኤግል እያለችም ሆነ አሁን ትልቁም ከተሠራ በኋላ የሦስቱም አገር ዜጐች የሆቴሉ ተጠቃሚዎች በመሆናቸው የእነሱን ቀልብ ለመሳብ የተደረገ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ሆቴሉ የተሠራው የከተማዋን ነዋሪ ከግምት ውስጥ በማስገባት ነው ያሉት አቶ አንዷለም፤ ከከተማው ነዋሪ በተጨማሪ ከሌላ ቦታም የሚመጣ ሰውና የውጭ አገር ቱሪስቶችም የሚስተናገዱበት እንደሆነ ያብራራሉ፡፡ “ቤቱ ደረጃውን የጠበቀ ነው፤ ነገር ግን ቢራ 17 ብር ይሸጣል፣ ድራፍት 13 ብር ነው ይሄ ቫትን ጨምሮ ነው” የሚሉት ስራ አስኪያጁ፤ ምግብም ቢሆን በ40 እና በ50 ብር መካከል መሆኑን ይናገራሉ፡፡ አልጋዎቹ ሶስት ደረጃ ያላቸውና ደረጃቸውን የጠበቁ ሲሆኑ ከ280 ብር እስከ 480 ብር ዋጋ ተተምኖላቸዋል፡፡ ይኼም አቅምን ግምት ውስጥ አስገብቶ የተተመነ እንደሆነ አቶ አንዷለም አጫውተውናል፡፡ ሆቴሉ በአሁኑ ሰዓት ለ235 ቋሚ ሠራተኞች የሥራ ዕድል ፈጥሯል፡፡ በአሁኑ ሰዓት በሆቴሉ የሰው ኃይል አስተዳደር ሆነው በኃላፊነት እየሠሩ የሚገኙት አቶ አቡ፤ የብዙ ሙያ ባለቤት ናቸው፡፡

ከመምህርነት ሙያ ጀምሮ በርካታ ሥራዎችን ሰርተዋል፡፡ በሆቴሉ የቅርፃቅርፆች ሥራ ላይ በስፋት የተሳተፉ ሲሆን በውስጣቸው የነበረውን የአርት ሙያ እዚህ ሆቴል ቅርፃቅርፆች ላይ እውን በማድረጋቸው ደስተኛ ናቸው፡፡ “በኤግል ሆቴል ግንባታ ውስጥ አንድም አርት ያልሆነ ነገር የለም” በማለት አስተያየታቸውን የጀመሩት አቶ አቡ፤ ኤግሏን ለመስራት በተለይ ማንቁርቷ በርካታ ጊዜ ፈርሶ እንደተሠራ ይገልፃሉ። ኤግል በአለም ላይ በርካታ ታሪኮች እንዳሏት የሚናገሩት አቶ አቡ፤ የጥንካሬ፣ የውበት፣ የጠንካራ እይታ እና የመሰል ጥራት መገለጫዎች መሆኗን ጠቁመው በአጠቃላይ ከሆቴሉ እቅድ ጀምሮ በአርቱም ላይ በመሳተፋቸው ጭምር ደስተኛ እንደሆኑም ይናገራሉ፡፡ አርቱ ከግንባታው ጐን ለጐን በተጓዳኝ የተሠራ በመሆኑ ቅርፃቅርፆቹም አራት ዓመት እንደፈጁ ነው የሚናገሩት፡፡ አቶ አቡ መምህር በነበሩበት ጊዜ አርት ስኩል ውስጥ የመማር እድል የገጠማቸው ቢሆንም እንደ አባታቸው ኢንጂነር የመሆን ፍላጐት ስለነበራቸው ትምህርታቸውን ማቋረጣቸውን ገልፀው፤ ሆኖም የአርት ፍቅራቸው እየጠነከረ ሲመጣ ከግርማችን ፒ ኤል ሲ ባለ ድርሻዎች አንዱ ሆነው ህልማቸውን እውን ለማድረግ በመብቃታቸው ደስተኛ ናቸው።

የግርማችን ፒኤልሲ ባለ አክሲዮኖች የቢዝነስ መሠረት ምንም እንኳ ሆቴል ቢሆንም በአሁኑ ሰዓት በትራንስፖርት ዘርፍ፣ በህንፃ መስታወት ገጠማና መሰል ቢዝነሶች መሠማራታቸውን አቶ አንዱአለም ይናገራሉ፡፡ አሁን ኤግል ሆቴል ካለበት ሥፍራ አጠገብ የማስፋፊያ ቦታ እየጠየቁ ነው፡፡ የመሰብሰቢያ አዳራሽ፣ የመዋኛ ሥፍራ፣ የህፃናት መጫወቻና አረጋውያን ለብቻቸው በትንሽ ክፍያ የሚዝናኑበት የራሣቸው የሆነ ደረጃውን የጠበቀ መዝናኛ የማሠራት ሀሣብ እንዳላቸው የግርማችን ፒ ኤል ሲ ባለድርሻዎች ይናገራሉ፡፡ “ስለ አረጋዊያኑ መዝናኛ ማሰባችንን ለእናታችን ስናጫውታት ‘ይህ ትልቁ ሐሣብ ነው’ በማለት ደስታዋን ገልፃልናለች” የሚሉት አቶ አንዷለም ፤ የጊዜ ጉዳይ እንጂ እንደሚሳካ ጥርጥር እንደሌላቸው ይናገራሉ፡፡ በአዳማ ከተማ ትልቅ የእንግዳ ማረፊያ በመገንባትም ላይ ይገኛል፡፡ አቶ አንዷለም እንዳጫወቱን፤ እንግዳ ማረፊያው አስራ ስምንት ክፍሎች የሚኖሩት ሲሆን አንዱ ክፍል መኝታ፣ ሳሎን፣ መታጠቢያና ማብሰያ ክፍሎችን ያጠቃልላል፡፡ እንግዳው የሚፈልገውን ነገር አብስሎ ለመመገብ እንዲችል የታሠበ ሲሆን እቃ ለመግዛት ሩቅ ሄዶ እንዳይቸገር በግቢው ውስጥ ደረጃውን የጠበቀ ሱፐር ማርኬት ይኖረዋል፡፡

የሚያበስልለት የሚፈልግ ከሆነም በገስት ሀውሱ ውስጥ ዝግጁ የሆኑ ሠራተኞች ይኖራሉ ተብሏል፡፡ ኤግል ሆቴል ፊት ለፊት አስፓልቱን ተሻግሮ “ናሽናል” የተሠኘ ታዋቂ ጭፈራ ቤት አለ፡፡ ጭፈራ ቤቱ በግርማችን ፒኤልሲ ባለቤትነት የሚመራ ነው፡፡ ይህ ጭፈራ ቤት ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ሊገነባ ዲዛይኑ አልቆ በጀት እንደተመደበለት የሚናገሩት አቶ አንዷለም፤ እጅግ ዘመናዊና የከተማዋን ደረጃ በጠበቀ መልኩ ሊሠራ ዝግጅቱ ተጠናቋል ብለዋል፡፡ የኤግል መኝታ ክፍሎች ውስጥ በሁለት አቅጣጫ ሲቆሙ ማለትም በምስራቅና በምዕራብ የከተማዋን የተለያዩ ገጽታዎች መቃኘት ይችላሉ። ለምሣሌ የመኝታ ክፍሎቹ ውስጥ ቆመው ወደ ምዕራብ ሲመለከቱ ከሆቴሉ ከምድር ቤቱ ባር ጀምሮ አጠቃላይ የሆቴሉን እንቅስቃሴ መቃኘት ይችላሉ፡፡

አሻግረው ሲመለከቱ ትልቁን ገልማ አባገዳ፣ የንፋስ ኃይል ማመንጫውን ተሽከርካሪና በርካታ የከተማዋን ክፍል ይመለከታሉ፡፡ ይህን ሆቴል በሚያስፋፉበት ጊዜ የገጠማቸው ችግር ምን እንደሆነ ጠይቀናቸው ሲመልሱ “አሁን ደስተኛ ብንሆንም በፊት ግን ፈተና የሆነብን ለማስፋፊያው ሲባል 11 አባወራዎች መነሣት ነበር” ይላሉ አቶ አንዷለም፡፡ ምንም እንኳ ይኖሩበት የነበረው ቤት በጣም ጠባብ ቢሆንም ከለመዱበት ቦታ ማስነሣቱ ፈታኝ እንደነበር አስታውሠው፤ ከከተማው መስተዳድር ጋር በመነጋገር ቦታ ተመርጦ ለእያንዳንዱ አባወራ 80ሺህ ብር በማውጣት አምስት አምስት ክፍል ቤት አሠርተው ማስረከባቸውን ገልፀዋል፡፡

ባለፈው ሳምንት በአፍሪካ የነፃነት፣ የህብረትና የአንድነት የትግል ታሪክ ውስጥ አንፀባራቂ ቦታ ከያዙት የአፍሪካ አንድነት መስራች አባት መሪዎች ውስጥ ግንባር ቀደም ናቸው ስለሚባሉት የጋናው የመጀመሪያ ፕሬዚዳንት የክዋሜ ንክሩማህን ግለ ስብዕና የሚያስተዋውቅ ጽሑፍ ማቅረቤ ይታወሳል። የአሁኑ ጽሑፌ የክዋሜ ንክሩማህን ከነፃነትና ከአንድነት ትግሉ በስተጀርባ የነበረ ማንነታቸውን በመጠኑ ያስቃኛል፡፡ ክዋሜ ንክሩማህ፤ አፍዝ አደንግዝ የሆነ ግርማ ሞገስና ከማንኛውም ሰው ጋር በቀላሉ የመግባባት አስደናቂ ችሎታ ቢኖራቸውም ያለ አንድ የቅርብ ጓደኛና ሚስጥረኛ አጋር እንደ በረዶ በሚቀዘቅዝ ብቸኝነት የሚኖሩ ሰው ነበሩ፡፡

ፕሬዚዳንት ንክሩማህ በስልጣን ላይ በነበሩበትም ሆነ ከዚያም በፊት ባሳለፉት ህይወታቸው ጥቂት የእረፍት ጊዜያቸውን ማሳለፍ የሚፈልጉት ከቅርብ የስራና የትግል ጓዶቻቸው ጋር ሳይሆን ከሴቶችና ከኮረዶች ጋር ብቻ ነበር፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ዋነኛ መዝናኛቸው ከነበረው ስራቸው ውጪ የንክሩማህ ልብ ስስ የነበረው ለሴቶች ብቻ ነው፡፡ በእርግጥም ንክሩማህ ከሴቶችና የደረሱ አፍላ ኮረዶች ጋር መቃበጥ ነፍሳቸው ነበር። እንዲህም ሆኖ ግን አለመጠን ተጠራጣሪ ሰው ከመሆናቸው የተነሳ፣ እንዲያ ከሚወዷቸው ሴቶችና ኮረዶች ጋር ጠበቅ ያለ የምር ወዳጅነት ለመመስረት እጅግ ይፈሩና ይጠነቀቁ ነበር፡፡ ትዳር ለመያዝ የሚሆን የአንዲት ደቂቃም እንኳ ጊዜ የለኝም በማለት በግልጽ ያወጁበት ዋነኛው ምክንያትም ይሄው ተጠራጣሪነታቸውና ፍርሃታቸው ነበር፡፡

ክዋሜ ንክሩማህ፣ ያኔ አብረዋቸው ይቃበጡ ከነበሩት በርካታ ሴቶችና ኮረዶች መካከል የተለየ ወዳጅነት መመስረት የቻሉት የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት የጋና አገረ ገዢ የነበሩት የሰር ቻርለስ አርደን ክላርክ ፀሐፊ ከነበረችው ወጣት እንግሊዛዊት ኤሪካ ፓወል ጋር ብቻ ነበር፡፡ ንክሩማህ ከሴቶች ጋር ዋዛ ፈዛዛ መውደዳቸውን አሳምራ የምታውቀው ኤሪካ ፓወል፣ ባልገመተችው ሁኔታና ጨርሶ ባልጠበቀችው ቀን በመኖሪያ ቤታቸው በክርስቲያንቦርግ ግንብ ራት ሲጋብዟት ግራ ከመጋባቷ የተነሳ ምን ብላ መመለስ እንዳለባት መወሰን አቅቷት ተቸግራና ተጨንቃ ነበር፡፡ በመጨረሻ ለአለቃዋ ለሰር ቻርለስ አርደን ክላርክ ስታማክራቸው፣ እርሳቸውም የንክሩማህን ሰብዕና ብጥርጥር አድርገው ስለሚያውቁት “ታውቂያለሽ ኤሪካ … ንክሩማህ እኮ ብቸኛ ሰው ነው፤ በጣም ብቸኛ ሰው” በማለት የቀረበላትን ግብዣ እንድትቀበል በዘወርዋሬ መክረው እንዳግባቧት የህይወት ዘመን ትዝታዋን ባሰፈረችበት መጽሐፏ ውስጥ ገልፃዋለች፡፡

በእራት ግብዣው የተጀመረው የኤሪካና የንክሩማህ ወዳጅነት፣ ቀስ በቀስ እየጠበቀ ስር መስደድ ሲጀምር ኤሪካ የሰር ቻርለስ የፀሐፊነት ስራዋን በመልቀቅ የንክሩማህ የግል ፀሐፊ ሆና ተቀጠረች፡፡ ይህንን ያየውና የሰማው ድፍን የአክራ ከተማ ነዋሪ፣ ኤሪካን የንክሩማህ ቅምጥ እንደሆነች ቢያወራባትም እርሷ ግን ግንኙነታቸው እስከተቋረጠበት እስከመጨረሻው ቀን ድረስ ሽምጥጥ አድርጋ ክዳዋለች፡፡ በሌላ በኩል፣ ደግሞ ኤሪካ ፓወል ከንክሩማህ ጋር የነበራትን ጠበቅ ያለ ግንኙነትና አብሮ ወጣ ገባ ማለት የተመለከቱ ጋናውያንና የውጭ ሀገር ዜጐች፣ ትዳር ሊመሠርቱ ይችላሉ ብለው በሰፊው ቢገምቱም ጉዳዩ ከግምት ማለፍ ሳይችል ቀርቷል፡፡ የሆኖ ሆኖ አብረው ባሳለፉት የፍቅር ጊዜያት ውስጥ ንክሩማህ ፀባያቸው እጅግ ተለዋዋጭ ከመሆኑ የተነሳ ጨርሶ የማይጨበጥ፣ ትዕግስት የለሽና፣ ግንፍልተኛ ሰው እንደሆኑ፣ አልፎ አልፎም የሚያፈቅሩትና የሚያፈቅራቸው ሰው እንደሌለ በመናገር ይነጫነጩ እንደነበር የገለፀችው ኤሪካ፤ አብረው እየተዝናኑ በነበረበት አንድ ምሽት ግን ንክሩማህ በምድር ላይ ከልባቸው የሚተማመኑባትና ለሁነኛ ምክር የሚመርጧት ብቸኛዋ ሰው እርሷ ብቻ እንደሆነች በደንብ እንደነገሯት በመጽሐፏ ይፋ አድርጋዋለች፡፡

ክዋሜ ንክሩማህ የማታ ማታም ቢሆን ትዳር ለመያዝ የሞከሩት በግማሽ ልባቸው ነበር። ለዚያውም ለትዳር የምትሆናቸውን ሴት ፍለጋ አይናቸው ያማተረው በሀገራቸው በጋና አልነበረም። የፕሬዚዳንትነት ስልጣናቸውን ጨብጠው ጥቂት ወራቶችን እንዳሳለፉ፣ አንድ ቀን ድንገት የቢሮአቸውን ስልክ አንስተው ሽርካቸው ለነበሩትና የፀረ ኮሎኒያሊዝምና ኒዎ ኮሎኒያሊዝም የትግል አጋሬ ለሚሏቸው የግብፁ መሪ ጋማል አብደል ናስር ደወሉላቸው፡፡ አጭር የወዳጅነት ሰላምታ ከተለዋወጡ በኋላ ናስር ጨርሰው ያልገመቱት፣ ያልጠበቁትና ዱብእዳ የሆነባቸውን ጥያቄ አወረዱባቸው፡፡ “ጓድ ናስር፤ እባክዎ በሀገርዎ በግብጽ ከሚገኙት ደማም ሸጋ ኮረዳዎች ውስጥ አንዷን ቆንጆ ይምረጡልኝና አግብቼ ጐጆ ልውጣ? እባክዎ ወዳጄ፤ እባክዎ ጓድ ፕሬዚዳንት፤ አንዷን ያገርዎን ልጅ ያጋቡኝና ለወግ ለማዕረግ ልብቃ” በማለት ለግብፁ ፕሬዚዳንት ጋል አብደል ናስር ተማጽኖአቸውን አቀረቡላቸው፡፡ ፕሬዚዳንት ንክሩማህ ይህን የትዳር ጥያቄያቸውን ሲያቀርቡ የቅርብ የትግልና የስራ ባልደረቦቻቸው ለነበሩት ጋናውያን ባለስልጣናት ትንፍሽ አላሉም ነበር፡፡ በአፍሪካ የነፃነት ትግል ውስጥ ስመጥርና የአንድ ሀገር መሪ ከሆነ ሰው በመቶ አመታት ጊዜ ውስጥ እንኳ ቢሆን ሊቀርብልኝ ይችላል ብለው ያልገመቱት ጥያቄ የቀረበላቸው ፕሬዚዳንት ናስር፣ ነገሩ በእጅጉ ቢያስገርማቸውም ንከሩህማን አላሳፈሯቸውም፡፡

የምንተ እፍረታቸውን የቅርብ አማካሪያቸውና የማስታወቂያ ምኒስትራቸው ከነበሩት ታዋቂው ግብጻዊ ጋዜጠኛ ሞሐመድ ሃይካል ጋር በመመካከር ፋቲያ ሪዝቅ የተባለች ቆንጆ ግብጻዊት አፈላልገው አጩላቸው። በጣት የሚቆጠሩ ታዳሚዎች ብቻ በተገኙበት በመኖሪያ ቤታቸው ክርስቲያንቦርግ ግንብ በተዘጋጀ እጥር ምጥን ያለ ድግስም ፕሬዚዳንት ንክሩማህ ተሞሽረው ጐጆ ወጡ - ግንቦት 30 ቀን 1957 ዓ.ም፡፡ የሰርጋቸው እለትም ፕሬዚዳንት ንክሩማህ ምን ሊያደርጉ እንዳሰቡ ለቢሮ ፀሐፊዎቻቸውም ሆነ ረዳቶቻቸው ምንም አይነት ፍንጭ አላሳዩም። ያለወትሮአቸው በሙሉ ጥቁር ሱፍ ልብስ፣ በነጭ ሸሚዝና ቀይ የቢራቢሮ ክራቫት ሽክ ብለው ዘንጠው ያያቸው የመቶ አለቃ ሃሚልተን የተባለ ልዩ ረዳታቸው “የክርስቶስ ያለህ! ፕሬዚዳንት ልክ እንደ ሙሽራ እኮ ነው ሽክ ዝንጥ ያሉት!” ሲላቸው፣ ንክሩማህ እንኳን መልስ ሊመልሱለትና ሙሽርነታቸውን ሊነግሩት ቀርቶ፣ የወትሮ ፈገግታቸውን እንኳ ሊያሳዩት አልፈለጉም፡፡ የመዳራቸውን ዜና የሰማው እንደተቀረው ጋናዊ በብሔራዊ ራዲዮ ጣቢያው የቀትር ዜና እወጃ ላይ ነበር፡፡

ክዋሜ ንክሩማህ ከፋቲያ ሪዝቅ ጋር የፈፀሙት የጋብቻ ህይወት አብዛኛውን ጊዜ በከፍተኛ ዝምታ የተሞላ ሲሆን አልፎ አልፎ ባልና ሚስቱ ለመግባባት የሚሞክሩት በአይንና በእጅ ምልክት ብቻ ነበር። ለምን ቢሉ … ጥንዶቹ የሚግባቡት የጋራ ቋንቋ ስላልነበራቸው ነው፡፡ ባለቤታቸው ፋቲያ ሪዝቅ፣ ከአረብኛና እጅና እግሩ ከማይያዝ የተሰባበረ የፈረንሳይኛ ቋንቋ በቀር ጆሮዋን ቢቆርጧት እንግሊዝኛ የማትሰማም የማትናገርም ነበረች፡፡ ንክሩማህም “ሽኩረን” (አመሠግናለሁ) ከሚለው የአረብኛ ቃል በቀር ሌላ ነገር አይሰሙም አይናገሩም ነበር፡፡ ፕሬዚዳንት ክዋሜ ንክሩማህ፣ ከፋቲያ ሪዝቅ ጋር የመሠረቱት ጋብቻ ሶስት ልጆችን ቢያስገኝላቸውም በ1965 ዓ.ም ለቀድሞ ወዳጃቸው ኤሪካ ፓወል በፃፉት ደብዳቤ፣ የያዙት ትዳር ከብቸኝነት ስሜታቸው ጨርሶ እንዳላላቀቃቸው እውነቱን ተናዘውላታል፡፡ “ኤሪካ ሚስት ማግባት ፈጽሞ እንደማልፈልግ ታውቂያለሽ፡፡ ለእኔ ብዬ ሳይሆን ለፕሬዚዳንትነቴ ስል ብቻ ሚስት እንዳገባሁ ነግሬሽ ነበርን?” በማለት ለኤሪካ ጽፈውላታል፡፡

እንዳሉትም ከሰርጋቸው ቀን በፊት ስሟን ሰምተውትም ሆነ አይኗን አይተውት ከማያውቁት ፋቲያ ሪዝቅ ጋር የመሠረቱትን ጋብቻ ለፕሬዚዳንትነታቸው ሲሉ ብቻ አክብረውት ኖረዋል፡፡ ብቃትንና ክህሎትን በተመለከተ ፕሬዚዳንት ክዋሜ ንክሩማህ፣ የሰልፍ ረድፋቸው ልበ ብርሀንና አዕምሮ ብሩህ ከሚባሉት ተርታ ነበር፡፡ በፖለቲካ ብቃትና ክህሎታቸው በመጠቀም ፈጽሞ አይነኬና ተገዳዳሪ አልባ ይባል የነበረውን የእንግሊዝ የቅኝ አገዛዝ ሀይል ፊት ለፊት በመጋፈጥ፣ የነፃነት ትግሉን በግንባር ቀደምትነት በማስተባበርና በመምራት አገራቸውን በ1957 ዓ.ም ማርች 6 ቀን ነፃነቷን እንድትጐናፀፍ አስችለዋታል፡፡ በክዋሜ ንክሩማህ የተመራው የጋና የነፃነት ትግልና ያስገኘው ውጤትም በእንግሊዝ ቅኝ አገዛዝ ስር ይማቅቁ ለነበሩት በርካታ የአፍሪካ ሀገራት የነፃነት መንገዱን ከፍቶላቸዋል፡፡ በዚህ መሠረትም በ1960ዎቹ አመታት ጋናን ተከትለው ሀያ ስምንት የአፍሪካ ሀገራት ከአውሮፓ የቅኝ አገዛዝ ለመላቀቅና ነፃነታቸውን ዳግመኛ ለመቀዳጀት በቅተዋል፡፡ ይህም ለፕሬዚዳንት ንክሩማህ በወቅቱ ነፃ የወጡ የበርካታ የአፍሪካ መሪዎችን ከፍተኛ አድናቆትና አክብሮትን አስገኝቶላቸው ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ይህ አክብሮትና አድናቆት በግል ከነበራቸው ከፍተኛ ፖለቲካዊ ፍላጐትና ምኞት ጋር ተዳምሮ፣ ከሌሎች የወቅቱ የአፍሪካ መሪዎች በአስተሣሠብም ሆነ በመሪነት ችሎታ የላቁና ከሁሉም የተለየ ሚና ለመጫወት በመለኮት ተመርጠው የተቀቡ መሲህ መሪ እንደሆኑ አድርገው ራሳቸውን እንዲቆጥሩ አደረጋቸው፡፡

በዚህ የተነሳም የሚመሯትን ሀገራቸውን ጋናን ከድሀና ኋላቀር ሀገርነት ወደ ኢንዱስትሪ ሀይልነት፤ የትምህርት ማዕከልና ሌሎች ሀገራት እንደርሷ ለመሆን የሚመኟት የሶሻሊስት ህብረተሠብና ሀገር ሞዴልነት ለመቀየር ቆርጠው ተነሱ፡፡ ከሀገራቸው ውጭም አፍሪካን በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚና፣ በወታደራዊ ሀይል ረገድ ታላቅ የሆነች፤ እንደ አሜሪካ አሊያም እንደያኔዋ ሶቪየት ህብረት የተባበረችና አንድ የሆነች ለማድረግና በፕሬዚዳንትነት ለመምራት ሌት ተቀን ማለም ጀመሩ፡፡ ማርክስና ኤንግልስ ለአውሮፓ፣ ማኦ ዜዱንግ ደግሞ ለቻይና እንዳበረከተው አይነት ፖለቲካዊ አስተዋጽኦ ለአፍሪካ ማበርከት የሚያስችል ልዩ ችሎታ አለኝ ብለው በእርግጠኛነት በማመናቸው “ንክሩማኒዝም” የተሰኘ የራሳቸውን ልዩ ርዕዮተ አለም በመቅረጽ በጋና በይፋ አወጁ፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠር የአሜሪካ ዶላር ወጪ በማድረግም ይህን ርዕዮተ አለማቸውን የሚያጠናና የሚያስፋፋ ትልቅ የምርምር ተቋም በስማቸው በመሠየም አቋቋሙ፡፡ ከፓርቲያቸው ቢሮዎች አንስቶ የወጣቶች፣ የሴቶች፣ የሰራተኞች፣ የሙያና ሌሎች የሲቪል ማህበራት “ንክሩኒዝም” የተሰኘውን ርዕዮተ አለማቸውን በከፍተኛ ንክሩማሀዊ ስሜትና ተነሳሽነት በመላው የጋና ምድርና የጋና ህብረተሠብ ዘንድ በሚገባ እንዲያሰርፁ ቀጭን ትዕዛዛ አስተላለፉ፡፡ ይህን ትዕዛዛቸውን ያለ አንዳች ማንገራገርና ተቃውሞ ተግባራዊ ለማድረግ በሁሉም አቅጣጫ እንቅስቃሴ መጀመሩን እንዳረጋገጡ፣ በፕሬዚዳንትነት ሊመሯት የቋመጡላትን የተባበረች አፍሪካን ወደ መፍጠሩ ህልማቸው ፊታቸውን አዞሩ፡፡

የሳምንት ሰው ይበለን!! “የተባበሩት የአፍሪካ መንግስት (United States of Africa) አሁኑኑ መፈጠር አለበት፡፡ ለዚህ አሁኑኑ መንቀሳቀስ አለብን፡፡ ለነገ ካልን እጅግ እንዘገያለን፡፡” በማለት የአፍሪካ ህብረት ወይም አንድነት ሳይሆን እንደ አሜሪካ ወይም እንደያኔዋ ሶቭየት ህብረት የተባበሩት የአፍሪካ መንግስት አሁኑኑ መፍጠር አለብን በለት በሙሉ ሃይላቸው ተንቀሳቅሰዋል፡፡ የዛሬ 50 አመት የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን ለመመስረት አዲስ አበባ ላይ በተካሄደው የመሪዎች ጉባኤ ላይም ይህን አቋማቸውን በማንሳት የተባበሩት የአፍሪካ መንግስት መመስረቱን ጉባኤው እንዲያውጅ በእጅጉ ወትውተው ነበር፡፡ ፕሬዚዳንት ንክሩማህ ይህን አቋማቸውንና ጥሪያቸውን በወቅቱ በጉባኤው ላይ ከነበሩት የአፍሪካ መሪዎች አንዳቸውም ስላልደገፉላቸው በብሽቀት ጨሰው ነበር፡፡ ያኔ ታንጋኒካ ትባል የነበረችው የታንዛንያ ፕሬዚዳንት ጁለየስ ኔሬሬ የተባበሩት የአፍሪካ መንግስት ከመመስረታችን በፊት ለምን የምስራቅ አፍሪካ መንግስታት ፌዴሬሽን አናቋቁምም የሚለውን ሃሳብ ሲያቀርቡማ ፕሬዚዳንት ንክሩማህ በከፍተኛ ብስጭት ፀጉራቸውን ሊነጩ ደረሱ፡፡

በዚህ ብቻም አላበቁም፡፡ ሃሳባቸውን የተቃወሟቸውን መሪዎች በተይም ፕሬዚዳንት ኔሬሬን “የማትረባ፣ ቀለም ያልዘለቀህ ገጠሬ” በማለት በቀጥታና በግልጽ ንቀት ወርፈቸዋል፡፡ ፕሬዚዳንት ንክሩማህ የነበራቸው ዲካ የለሽ የበላይነት ስሜት እርሳቸው ያቀረቡትን ማናቸውም አይነት ሃሳብ የየትኛውም የአፍሪካ ሀገር መሪ ያጣጥልብኛል ብለው እንዳያስቡ አድርጓቸው ነበር፡፡ እናም ያኔ በመጀመሪያው የመሪዎች ጉባኤ ላይ የገጠማቸውን ተቃውሞ በልበ ሰፊነት ለመቀበል አቅምና ቀልባቸውን ነሳቸው፡፡ ፕሬዚዳንት ንክሩማህ የተጠናወታቸው ወደር የሌለው የበላይነት ስሜት እጅግ ከፍተኛ ለሆነ ልታይ ልታይ ባይነት ልክፍት አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ እናም ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ከሁሉም የበለጡና የላቁ መስለው ለመታየትና የሚመለከታቸውን ሰው ሁሉ ቀልብ ለመማረክ የማያደርጉት ነገር አልነበረም፡፡ ይህንን የበላይነትና ልታይ ባይነት ከፍተኛ ስሜታቸውን በሚገባ የተረዳው የፓርቲያቸውና የመንግስታቸው የፕሮፖጋንዳ ማሽንም የዋና አለቃውን ስሜትና ፍላጐት ለማርካት ያልተጓዘው ርቀት ያልፈነቀለው ድንጋይ ጨርሶ አይገኝም፡፡

ለምሳሌ በንክሩማህ የሚመራህ Convention People’s Party ልሳን የሆነው evening News የተሰኘው ጋዜጣ በሰኔ 19 ቀን 1954 ዓ.ም እትሙ ንክሩማህን የገለፃቸው “ንክሩማህ ማለት መለኮታዊ ሃይል ያለው፣ ነብይ፣ ህዝቡን ወደ ተቀደሰችው የነፃነት መሬት የሚመራ አዲሱ ሙሴ፣ የአፍሪካ ኮከብ፣ ድሀና ጐስቋላ የሆኑ በሚሊወን የሚቆጠሩ ጥቁሮች ተስፋ፣ የገና መሲህ፣ ብረቱ ልጅና፣ የጐዳና ተዳዳሪ ወጣቶች ታላቁ መሪ” በማለት ነበር፡፡ በየእለቱ እየታተሙ የሚወጡ የመንግስት ጋዜጦችም ከርዕሰ አንቀጽ እስከ ተራ የዜና ዘገባቸው ድረስ ዋነኛ ትኩረታቸው የክዋሜ ንክሩማህን የአዕምሮ ምጡቅነትና አርቆ አሳቢነት በተቻላቸው አቅም ሁሉ ማራገብ ብቻ ነበር፡፡ በ1961 ዓ.ም ንክሩማህን አስመልክቶ የጋና መንግስት በይፋ ያወጣው መግለጫ እንዲህ ይላል “በሚሊወን ለሚቆጠሩ በአፍሪካ አህጉር ውስጥና ከአፍሪካ አህጉር ውጪ ለሚኖሩ ህዝቦች ክዋሜ ንክሩማህ ማለት አፍሪካ ማለት ነው፡፡

አፍሪካ ማለት ደግሞ ክዋሜ ንክሩማህ ማለት ነው፡፡ በአፍሪካ ምን እየተካሄደ ነው የሚል ጥያቄ ቢቀርብ ሁሉም ሰው መልሱን ለማግኘት የሚሮጠው ወደ አንድ ሰው ብቻ ነው ወደ ክዋሜ ንክሩማህ፡፡ ለኢምፔሪያሊስቶችና ቅኝ ገዢዎች የንክሩማህ ስም ከንፈራቸው ላይ ያለ እርግማን ማለት ነው፡፡ ለመጤ ሰፋሪ ነጮች ደግሞ በአፍሪካውያን ኪሳራ ያሳለፉት የምቾትና የድሎት ጊዜ ማክተሙን የሚጠቁም የማስጠንቀቂያ ደወል ማለት ነው፡፡ በውጭ የበላይነት ለሚማቅቁት አፍሪካውያን ግን የንክሩማህ ስም የተስፋ እስትንፋስና ነፃነት ማለት ነው፡፡ ክዋሜ ንክሩህ ማለት መላ ህይወታችን ማለት ነው፡፡ ያለእርሱ በህይወት መቆየት ጨረሶ አንቺልም፡፡” አሁን አንድ ቀላል ጥያቄ እንጠይቅ፡፡ ለመሆኑ እንዲህ የተባለላቸው የጋናው ፕሬዚዳንት ክዋሜ ንክሩህ የአመራር ብቃትና ክህሎታቸው እንዴት ያለ ነበረ? የሳምንት ሰው ይበለን፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ
Saturday, 01 June 2013 13:38

የመግደል ጥበብ

ምዕራፍ አንድ፡- በሬ ከአራጁ ይውላል ‘You are a murderer whether you know it or not’ ይህን አረፍተ ነገር ያገኘሁት አንድ ለዳጄ ያዋሠኝ መፅሐፍ ላይ ነው፡፡ መፅሐፉ ለኢ-ልብ ወለድ ፀሐፊዎች እና አንባቢዎች የተፃፈ ነው፤ The Art of Non Fiction ይላል (የፅሁፌን ርእስ ያስተውሏል፤ የመግደል ጥበብ ነው የሚለው፤ The Art of Homicide እንደማለት ነው)፡፡ መፅሐፉ የቲዎሪ፣ የጋዜጣ እና በሁለቱ መካከል ላይ የ middle range መጣጥፎችን በጥሩ ሁኔታ ለመፃፍ እና እነዚህን ፅሑፎች በጥሩ ሁኔታ ለማንበብ ተብሎ የተፃፈ ነው፡፡ የመፅሐፉ ፀሐፊ ይህን አረፍተ ነገር እንደ ምሳሌ የጠቀሰችው፣ የመጣጥፍ መግቢያ ላይ እንዲህ አይነት አረፍተ ነገር ብንጠቀም እንዴት አትኩሮት መሳብ እንደምንችል ለማሳየት ነው፡፡ በርግጥም አትኩሮት ይስባል፤ “አወቃችሁትም አላወቃችሁትም ሁላችሁም ነፍስ አጥፊዎች ናችሁ፡፡”

ሲባል የማን ቀልብ ነው የማይሳብ? የገዳይንም፤ የህይወት አፍቃሪ እና አክባሪንም፣ ቀልብ እኩል ይስባል፡፡ በተለይ የገዳይን ሳይሆን የህይወት አፍቃሪ እና አክባሪን ቀልብ የበለጠ ይስባል፡፡ ንፁህ ሠው አውቀህም ሆነ ሳታውቅ ነብስ አጥፊ ነህ ሲባል … ግልፅ ነው፤ ቀልቡ ይሳባል ብቻ ሳይሆን ይደነግጣል፡፡ ገዳይ ያው ገዳይ ነው “መግደል” የሚባል ነገር ያለበት ነገር ሁሉ አትኩሮቱን ይስበዋል፡፡ እኔ ግን ‘You are a murderer whether you know it or not’ የሚለውን እንደመግቢያ የተጠቀምኩበት አትኩሮት ለመሳብ ብዬ አይደለም። ሠው ገድዬ ነው፡፡ ይህን ፅሑፍ የፃፍኩት ከቀብር መልስ ነው፡፡ ሰውየውን የገደልኩት እኔ ነኝ፤ አገዳደሌ ግን ረቀቅ ያለ ስለሆነ እኔ ነኝ የገደልኩት ብዬ ለፖሊስ እጄን ብሰጥ ይስቁብኛል፤ እብድ ነው ብለው ይሳለቁብኛል፤ ስለዚህ ልብ-ወለድ ነው ብዬ መጻፍን መረጥኩ፡፡ በሬ ከአራጁ ይውላል ያልኩለትን ሠውዬ የተዋወቅሁት እሱ የ67 አመት እኔ የ37 ዓመት ሠዎች ሆነን ነው፡፡ ፀጉሩ ሙሉ ነጭ ነው፡፡ አይኖቹ የህፃን ልጅ ይመስላሉ፡፡ ቀጫጫ ነው፡፡ እድሜው አልታየኝም ነበር፡፡ ሠውየውን የወደድኩት ገና እንዳየሁት ነበር፡፡ እጅግ ውስብስብ በሆነ ሁኔታ ከስራ ተባርሬአለሁ፡፡

ተቀማጭ ገንዘብ ስለሌለኝ እና ጠጪ ስለነበርኩ፣ በአንድ ጊዜ ነው ከትልልቆቹ መደብር ወደ አረቄ መንደር የወረድኩት፤ እና የመጀመሪያውን አረቄ ስቀምስ እና ሠውየውን ቀና ብዬ ሳየው የሆነ ምስጢራዊ ስሜት ተሠማኝ፡፡ ከሠውየው ጋር እንደ ተያየን ደንግጠናል፤ ተዋደናል፤ እንደተዋደድን ሁለታችንም አውቀናል፡፡ ለመነጋገር ብዙ ጊዜ ወሰደብን፡፡ ሁልጊዜ ግን ሳናወራ እናወራ ነበር፡፡ ሠውየው ለምሳሌ እንዲህ ይላል፡፡ “እኔ እኮ አብዲሳ …” ስሙን ማንም ሳይነግረኝ አወቅሁት፡፡ (ስሙን አስተዋወቀኝ) ሲያወሩ ብዙ ጊዜ ‘እኔ እኮ እከሌ…’ እንደሚሉት አይነት ሰዎች አይደለም፡፡ የራሱን ስም ሲጠራ ራሱ አፉ ላይ ባዕድ ይሆንበታል፡፡ እራሳቸውን ደጋግመው እንደሚጠሩ እና እንደሚያደንቁ አይነት አይደለም፡፡ ያኔ “እኔ እኮ አብዲሳ…” ሲል የነበረው ስሙን እኔ እንዳውቅለት ነበር፡፡ ሠውየው አረቄ ቤት ስንት ሠዓት እንደሚመጣ፣ ስንት አረቄ እንደሚጠጣ፣ ስንት ሠዓት እንደሚወጣ አውቃለሁ፡፡ እሱም የእኔን እንደሚያውቅ ያስታውቅበታል፡፡

ምዕራፍ ሁለት፡- “ለምንድነው የምትወደኝ?” አንድ ቀን ስካር አድሮብኝ በጠዋት አረቄ ቤት ሄድኩ፡፡ ቁርስ አልበላሁም ነበር፤ እንቀጠቀጥም ነበር፡፡ የመጀመሪያውን መለኪያ ስጠጣ መረጋጋት ጀመርኩ፡፡ “ይኸውላችሁ ልጆች ሠው አትናቁ” አለ ሽማግሌው ለሌላ ሠው እያወራ ያለ ይመስላል፤ ግን እኔን ነበር የሚያየው፤ ወይም እኔን እያየ ለሌላ ሠው የሚያወራ ነበር የሚመስለው፤ ሀቁ ግን እኔን እያየ ለእኔ ነበር የሚያወራው፡፡ አየሁት እና ከት ብዬ ሳቅሁ፡፡ ሁሉም አፈጠጡብኝ፡፡ ሁሉም ሠካራሞች በጠዋት ተስፋ በቆረጡ እና በሚያስቆርጡ የሠካራም አይኖቻቸው አፈጠጡብኝ፡፡ ድንገተኛ፣ ደባሪ ፀጥታ ሠፈነ፡፡ “ምን ያስቅሃል?” አለኝ ሽማግሌው፡፡ “ሠው አልንቅም እኔ!” “ሠው ትንቃለህ ማን አለህ?” “አብዲሳ” “ስሜን ማን ነገረህ?” “አንተ፤ ማለቴ እራሶት” (አንተ፣ አንቱ ስል ድምፄ ውስጥ ማመንታት የለም፤ አማራጭ ነው ያለው፤ የቱን ልበልህ አንተ ወይስ አንቱ ነው፡፡) “መቼ? መቼ ቀን ነገርኩህ?” “ሀምሌ አስራ አንድ ቀን” “ጎበዝ ልጅ፡፡ እኔም አስታውሳለሁ፡፡

ሠው እንደማትንቅ ይህ ብቻ በቂ ነው፡፡ የዚያን እለት ለሀምሌ ሚካኤል አጥቢያ አስሬ አብዲሳ ስል የነበረው አንተ ስሜን እንድታውቅ ስለፈልግሁ ነበር፤ የዚያን እለት ስታየኝ አስተያየትህ ‘ስምህ ማነው?’ የምትል ይመስል ነበር፡፡ አብዲሳ ማለት ተስፋዬ ማለት ነው፡፡” “አውቃለሁ” “ማን ነገረህ?” “አንተ በለኝ፤ አጠራጠረህ እና አስተያየትህ ውስጥ ክብር ስለለ እሱ ይበቃል” “አመሰግናለሁ አብዲሳ” “በል ተነስ አሁን፤ ቁርስ ስላልበላህ ቁርስ ልግዛልህ” ተያይዘን ቁርስ ልንበላ ወጣን፡፡ ሰንጋ ተራ ቶታል ጋ ያለው ምግብ ቤት ሄድን፡፡ “ቁርስ ምን ልግዛልህ?” “’ምን ልግዛልህ’ አይባልም፤ ልጋብዝህ ነው የሚባለው” “አንተ እራስህ ነህ ይህን አባባል የምትጠቀመው፤ ካንተ ነው የተማርኩት፡፡ አረቄ ቤት ሰው ስትጋብዝ ‘አረቄ ልግዛልህ ወይ?’ ነው የምትለው፤ ልጋብዝህ አትልም” አስተናጋጁ መጥቶ አጠገባችን ዣንጥላ ሆኖ ቆመ፡፡ “ጋሽ አብዲሳ ምን ላምጣ?” “ለኔ የተለመደውን፤ ለዚህ ሠውዬ የሚፈልገውን ጠይቀው” “እሺ?” አለኝ አስተናጋጁ፡፡ “አብዲሳ የለመደውን አምጣልኝ” “ላንተ አይሆንም” አለ አብዲሳ፡፡

“እንዴት?” “የእንቁላል አለርጂ አለብህ” “እንዴት አወቅህ?” “ስታወራ ሰምቼ ነው፤ ከአሁን በኋላ እንዴት አወቅህ የሚለውን እንተወው” ሳናወራ እያወራን ነበር የኖርነው፡፡ ትንሽ ዝም ከተባባልን በኋላ፡- “አንድ ነገር ልጠይቅህ፤ የሚጠየቅ አይደለም፤ ግን ልጠይቅህ” አለኝ ሽማግሌው፡፡ “መልካም” “እንደምትወደኝ አውቃለሁ፤ ማወቅ የፈለግሁት ለምን እንደሆነ ነው፡፡ ለምንድነው የምትወደኝ?” “እኔ ሠው ወድጄ አላውቅም” “እኔን ግን ትወደኛለህ አይደል?” “አዎ” “ለምን?” “ፊትህ በጣም ይገርማል፤ ሀጢአት የምታውቅ አትመስልም፤ ፀፀት የለበትም ፊትህ፤ ፀፀት ብቻ ሣይሆን ሥጋትም የለበትም፤ ይገርማል፤ እንዲህ አይነት ፊት ያላቸው ሰዎች የሉም፡፡ አይንህን ሳየው ሁሌ እረጋጋለሁ፡፡ እንደ አንተ አይነት ንፁህ አይኖች አይቼ አላውቅም፡፡” “ስለኔ ሳይሆን ስለ ራስህ የምታወራ ነው የሚመስለው” “ለዚያ አይመስልህም ታዲያ የምወድህ?” “ስለ አይን ስታወራ አስደገነጥከኝ፤ አይኔ ውስጥ ጭካኔ አለ?” “የለም፤ ሙቀት ነው ያለው” “ያንተ አይን ውስጥ ግን አለ፤ ጭካኔ አለ” “ጭካኔ አይደለም” አልኩ በእርግጠኝነት፡፡

“አዎ፤ ጭካኔ አይደለም፤ ግራ ይገባል፤ ጭካኔ ይመስላል ግን ያስፈራል፤ ሠው ስታይ ታስፈራለህ” “አውቃለሁ፤ አስራ አንደኛ ክፍል እያለሁ ጌታቸው የሚባል እንግሊዝኛ አስተማሪያችን ስታየኝ ስለማልወድ እኔ ክፍል ውስጥ አትግባ ብሎ ለምኖኝ፣ እኔ እሱ ክፍል ላልገባ እሱ ጥሩ ውጤት ሊሰጠኝ ተስማምተን አድርገነዋል፡፡ ኮሌጅ እያለሁ፣ ነፍሱን ይማረውና ኤፍሬም የሚባል ሲቪክስ አስተማሪያችን ‘ምናባህ ታፈጥብኛለህ፤ የምፈራህ መሰለህ?!’ ብሎ ተማሪ ሁሉ እስኪታዘበው ጮኋል፡፡ ሰዎች ሳያቸው ይረበሻሉ” ለረዥም ጊዜ ዝም አልን፡፡ በዝምታችን ቆይታ፣ ሽማግሌው እያየሁት ፀዳሉ ፈካ፡፡

“ታውቃለህ…” አለኝ አለመጠን ተደስቶ እና ኮርቶ፡- “ታውቃለህ አሁን አይደለም የመጣልኝ፤ አይንህ ውስጥ ስላለው ነገር ካየሁህ ቀን ጀምሮ ነበር አስብ የነበረው፤ ሁሌ አስብ ነበር፤ ብታምንም ባታምንም በህልሜ አይኖችህን ብቻ አይ ነበር፤ አይኖችህን ብቻ፤ አሁን ደረስኩበት፤ አይኖችህ ውስጥ ምን እንዳለ ታውቃለህ?” “አውቃለሁ” ምን እንደሆነ ሳልነግረው ተሽቀዳድሞ “ቆይ እኔ ነኝ እምነግርህ፤ የሚገርምህ ግኝት ነው፤ አይኖችህ ውስጥ ያለው እርግጠኛነት ነው፤ ታይቶ የማይታወቅ እርግጠኝነት አይኖችህ ውስጥ አለ” “በትክክል ተመልሷል” ማስታወሻ የመያዝ ልማድ አለኝ፤ ሁሌ ከእጄ የማይጠፋ አፈርማ ቀለም ያለው ማስታወሻ ደብተር አለኝ፡፡ በጣም አጠር ያለ ማስታወሻ ስለምወስድ ይህ ማስታወሻ ደብተር እጄ ላይ ከርሟል፤ ገና ይከርማል፡፡ አሁን ከሽማግሌው ጋር ያወራናቸውን እና የማረኩኝን አንዳንድ ነገሮች ማስታወሻዬ ላይ አሰፈርኩ፡፡ እንደጨረስኩ ሽማግሌው፡- “ይህቺ ነገር ከእጅህ አትጠፋምና!” አለኝ፡፡

“አዎ፤ ላስታውሳቸው የምፈልጋቸውን ነገሮች እከትብብታለሁ” አልኩት፡፡ ምዕራፍ ሶስት፡- “ሠው ጤፉ” እኔ እና ጤፍ ኢትዮጵያዊ እና እንጀራ ተመጋቢ ከመሆነ የዘለለ ቅርርብ አለን፤ “ሠው-ጤፉ” እየተባልኩ ነው ያደግሁት፡፡ እናቴ ጎረቤቶቿ ተፅእኖ የሚያሳርፉባት አይነት ሴት አልነበረችም፡፡ ቡና ከጎረቤት ጋር አትጠራራም፤ ማህበር (ፅዋ) አትጠጣም፤ እቁብ አትሰበሰብም፣ አትጥልም ነበር፡፡ እድር ውስጥ የነበረችውም ግድ ሆኖባት ነው፡፡ እናቴ ለተፅእኖ አትመችም፡፡ ልጅ ሆኜ ከጓደኞቼ ጋር ስጫወትም (ከምወደው ልጅ ጋር እጫወታለሁ፤ ከማልወደው ጋር አልጫወትም) ሆነ ስጣላ ከቁብ የማስገባው ልጆቹን እና አቅሜን ነው፡፡ ልጆቹ ነገር ከፈለጉኝ ቤተሰቦቻቸውን ፈርቼ አልተዋቸውም፤ እላቸዋለሁ። ስጣላ ታዲያ ከፍተኛ ፀብ ነው የሚሆነው፡፡ በእድሜ እና በጥንካሬ የሚበልጡኝን ከቅርብ ከሆነ እናከሳለሁ፤ ከሩቅ ከሆነ፤ እፈናከታለሁ፡፡ እኩዮቼን በቦክስ እና በጠረባ እዘርራለሁ፡፡

ከደፋርነቴ እና ከዘደኝነቴ ሁሉ ልቆ ያስከበረኝ ቂመኝነቴ ነው፤ ቂም አልረሳም፡፡ ልጆች ብዙ ጊዜ ትምሕርት ቤት ተጣልተው ‘ቆይ ሰኔ ሰላሳ ላግኝህ’ ሲሉ ዝም ብለው ማስፈራራታቸው ነው፤ የአፍ-ልማድ ሆኖባቸው፤ የምራቸውን አይደለም፡፡ እኔ ግን ‘ሰኔ ሰላሳ ላግኝህ’ ካልኩ በቃ እንዲያ ማለቴ ነው፡፡ ሰኔ ሰላሳ ብዙ ጊዜ ቢዚ ነበርኩ፡፡ ታላቅ ወንድም አለኝ ብሎ ወይም በቤተሰቦቹ ተመክቶ የሚጣላኝ ብዙ የለም፡፡ ለዚያ እናቴ አለች። ማን እንደ ነገራት፣ እንዴት እንደ ደረሰችበት ባላውቅም ያለ ምክንያት ወይም በሰንካላ ምክንያት እንደማልጣላ ታውቃለች፡፡ የጎረቤት እናቶች እና አባቶች አባብለውም ተቆጥተውም አይልኩኝም፤ መቼ ሰምቻቸው። ታላቅ ለምን እንደሚከበር አይገባኝም ነበር፤ ብዙዎቹ የሚከበሩ አልነበሩም፡፡ ሲልኩኝ እምቢ ስል ከመቱኝ እማታለሁ፤ ከተቆጡኝ አንጓጥጣለሁ፤ ከሰደቡኝ ጆሮዋቸው ሞልቶ እስኪፈስ ብዙ ነገር እላቸዋለሁ፤ ስድብ አይደለም፤ አልሰድባቸውም፤ ለኔ እንደሚመስሉኝ እነግራቸዋለሁ፤ ብዙ ጊዜ ልክ ነበርኩ፡፡ ‘ሠው-ጤፉ’ የሚለው ስም የወጣልኝ ያኔ ነው፡፡

መጀመሪያ ማን እንዲያ እንዳለኝ አስታውሳለሁ፡፡ ወ/ሮ አበበች ነበሩ። (ሊልኩኝ ፈልገው አመናጭቀው በንቀት ሲጣሩ በጣቴ ምልክት ሰደብኳቸው፡፡ በጣም የተከበሩ ሴት ነበሩ፤ ቴሌቪዥን ነበራቸው፤ ሁሉም ልጅ ሳይጠሩት ሊላካቸው ይፈልጋል፤ እናም ሁሌም የኔ ኩራት፣ አለመታዘዝ ከሁሉም በላይ ያናድዳቸው ነበር፡፡) ከዚያ በኋላ ስሜ ሆኖ ቀረ፡፡ እናቴም ደስ ሲላት “ሠው-ጤፉ” ትለኝ ነበር እየሳቀች፤ አናቴን እየዳበሰች፡፡ አቤት ደስ ሲለኝ፣ እሷ እንዲያ ብላ ስትጠራኝ፡፡ “ሠው ጤፉ” ብሎ ፈሊጥ ይገርመኛል፡፡ ሌላ ቦታ፣ ከሌላ ሠው ሠምቼው አላውቅም፤ የትም ቦታ አንብቤው አላውቅም፡፡ ሁሌ እንጀራ ስለምበላ ሁሌ ትዝ ይለኛል፤ ሁሌ ፈገግ እላለሁ፡፡ “ሠው-ጤፉ” የሚገርም ንፅፅር ነው፤ የጤፍ ቅንጣት እና የበቆሎ ፍሬ እራሱ ከባድ ንፅፅር ነው፡፡ ለዚያውም ለሰባት ዓመት ልጅ የዋለ ንፅፅር ሲሆን ይገዝፋል፡፡ ወይዘሮ አበበችን አሁን አከበርኳቸው፡፡ (ይቀጥላል)

Published in ልብ-ወለድ

እንግዶች በመሳፍንትና በመኳንንት ቤቶች አርፈዋል ሁፌት ቧኜ አውሮፕላን ስለማይወዱ በመርከብና በባቡር ነበር የመጡት

የኋላ ማርሽ አስገብተን ወደ ዛሬ 51 ዓመት እንጓዝ፡፡ ብዙዎቹ የአፍሪካ አገራት ከቅኝ አገዛዝ ነፃ የወጡበት ጊዜ ነበር፡፡ ነፃ ያልወጡም አገራት ነበሩ፡፡ አፍሪካ ተባብራ ችግሮቿን እንድትፈታ፣ ነፃነቷንም እንድታስከብርና ነፃ ያልወጡ አገራትን እንድትደግፍ፣ በአንድነት የምንትቀሳቀስበት ኅብረት ያስፈልጋታል በማለት የፓን አፍሪካኒዝም የሚቀነቀንበት ወቅት ነበር፡፡ ከብዙ ጥረት በኋላ ሐሳቡ ተቀባይነት አገኘና የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዲመሠረት ነፃ የአፍሪካ መንግሥታት ተስማሙ፡፡

ነገር ግን ማን አስተባባሮ ድርጅቱ ይመሥረት? ቻርተሩንስ ማን ያዘጋጀው? የድርጅቱ መቀመጫስ የት ይሁን? … የሚሉት ምላሽ የሚሹ ጥያቄዎች ነበሩ።

በዚህ ጊዜ ኢትዮጵያ እኔ ኃላፊነቱን እወጣለሁ አለች፡፡ ይኼኔ ከየአካባቢው ተቃውሞ ተነሳ፡፡ “ኢትዮጵያ መሰብሰቢያ አዳራሽ፣ ሆቴል፤ መንገድ፤ ንፅህና፣ … የላትም፡፡ ካይሮ፣ ሌጐስ፣ ናይሮቢ፣ … እያሉ እንዴት አዲስ አበባ መቀመጫ ትሆናለች? በማለት የተቃወሙ ፖለቲከኞች ብዙ ናቸው፡፡ ነገር ግን ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ በነበራቸው ብልህ ፖለቲካዊ ብስለት፣ ከፍተኛ ጥረትና የማሳመን ችሎታ፣ አዲስ አበባ ከ51 ዓመት በፊት በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ የአፍሪካን አንድነት ድርጅት ምሥረታ ጉባኤ እንድታዘጋጅ ተወሰነ፡፡ ከውሳኔው በኋላ ጃንሆይ የካቢኔ ሚኒስትሮቻቸውን ሰብስበው፣ ጉዳዩን ካስረዱ በኋላ “ጊዜ የለንም፤ ያሉን 12 ወራት ብቻ ናቸው። የአውሮፕላን ማረፊያ ሜዳ፣ መሪዎች ሲመጡ የሚያርፉበትና የሚሰበሰቡበት አዳራሽ የለም። ጎበዝ! እንዴት ይህን ኃላፊነት እንወጣ? በማለት ጠየቁ፡፡ ለዝግጅት የተሰጠው ጊዜ በጣም አጭር ነው፡፡

ለምን ስብሰባው ለሌላ ጊዜ አይተላለፍም? በማለት ሐሳብ ያቀረቡ ሚኒስትሮች ነበሩ፡፡ ልዑል ራስ መንገሻ ስዩም (በወቅቱ ደጃዝማች) “ዕድሉ ሊያመልጠን አይገባም፡፡ ገንዘቡ ከተፈቀደልኝ በተባለው ጊዜ ውስጥ (እንዲያውም ከዚያ ቀደም ብዬ በዘጠኝና በአስር ወር) ሥራውን አጠናቅቄ አስረክባለሁ” በማለት ቃል ገቡ፡፡ ንጉሡም፣ ልዑል ራስ መንገሻ የተግባር ሰው መሆናቸውን ስለሚያውቁ “መንገሻ አደርገዋለሁ ካለ ያደርገዋል” በማለት በሐሳባቸው ተስማሙ፡፡ “ሥራው ወዲያውኑ ተጀምሮ ሌት ተቀን እየተሠራ የቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ፣ የአፍሪካ አዳራሽና የግዮን ሆቴል ተሠርተው ስላለቁ፣ ጉድ ተባለ፡፡ ልዑል ራስ መንገሻም “ልጄ ተባረክ” በመባል በንጉሡ ተመሰገኑ ያሉት በወቅቱ የፓርላማ አባል የነበሩት ፊታውራሪ አበበ ሥዩም ደስታ ናቸው፡፡

ፊታውራሪ አበበ ሥዩም የዛሬ 50 ዓመት የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሲመሠረት በፓርላማ ሕግ መምሪያ ም/ቤት የተንቤን ሕዝብ እንደራሴና የበጀት ኮሚቴ ሊቀመንበር ነበሩ፡፡ ስለ አፍሪካ አንድነት ድርጅት ምሥረታ፣ ስለ እንግዶቹ አቀባበልና ዝግጅት፣ … የሚናገሩት አላቸው። ዛሬ ፊታውራሪ አበበ የ83 ዓመት አዛውንት ናቸው። በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ በዝርዝር ሲናገሩ የማስታወስ ችሎታቸው ይደንቃል፡፡ ከ50 ዓመት በፊት የነበረውን ነገር ከዓመትና ከሁለት ዓመት በፊት እንደተፈፀመ ታሪክ ነው የሚያንበለብሉት፡፡ የሕይወት ታሪካቸውንም ጽፈው “ዝክረ ሕይወት” በሚል ርዕስ አሳትመዋል፡፡

ፊታውራሪ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የተመሠረተው እንዴት እንደነበር ያጫውቱናል፤ እንከታተላቸው፡፡ በዚያን ጊዜ አፄ ኃይለ ሥላሴ አፍሪካን አንድ የማድረግ ሕልም ነበራቸውና ሕልማቸው ተሳካ። በንጉሡ ዙሪያ የተሰባሰቡት ሚኒስትሮች በሳል ዲፕሎማቶች ነበሩ፡፡ ካቢኔው የሚመራው በጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀ/ወልድ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት ክቡር ከተማ ይፍሩ የውጭ ጉዳይ ሚ/ር፣ ክቡር ዶ/ር ተስፋዬ ገ/እግዚ የማስታወቂያ ሚ/ር፣ ክቡር ዶ/ር ምናሴ ኃይሌ፤ ክቡር አቶ ሰይፉ ማኅተመ ሥላሴ፣ እንዲሁም አፈ-ንጉሥ ተሾመ … የሚባሉ ሚኒስትሮች ወደ ተለያዩ የአፍሪካ አገሮች እየሄዱ ሲያስተባብሩና ሲያግባቡ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት ብዙ ተደማጭነት የነበራቸው የግብፁ መሪ ጋማል አብዱልናስር ነበሩ፡፡ እሳቸውን ለማግባባት ከፍተኛ ጥረት ተደርጓል፡፡ ይኼው የማግባባት ጥረት ተሳክቶ ስብሰባው በአዲስ አበባ እንዲካሄድ ሲወሰን እንግዶቹ መጥተው የሚሰበሰቡበት አዳራሽ፣ የሚያርፉበት ሆቴል፣ የለም፡፡ የተሰጠን ጊዜ ደግሞ አንድ ዓመት ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ ካላዘጋጀን ዕድሉ ለሌላ ይተላለፋልና ምን ይደረግ? ተባለ።

የሲዳሞ ጠቅላይ ገዥ የነበሩት ክቡር ደጃዝማች መንገሻ ሥዩም የሥራና መገናኛ ሚኒስትር ሆነው ስለተሾሙ፣ “ገንዘብ ከተሰጠኝ በአንድ ዓመት ውስጥ አይደለም፤ በዘጠኝ ወር ግፋ ቢል በአስር ወር ጨርሼ አስረክባለሁ” በማለት ለጃንሆይ ቃል ገቡ፡፡ “መንገሻ አያደርግም አይባልም፤ ይሠራል” ተባለ፡፡ የገንዘብ ሚ/ር የነበሩት እነ ክቡር አቶ ይልማ ዴሬሳና አንዳንድ ሚኒስትሮች “ይኼ እንዴት ይሆናል?” በማለት ጥያቄ አንስተው ነበር፡፡ ሥራው ተጀምሮ የቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፍያና የአፍሪካ አዳራሽ የተሠራው ያኔ ነው፡፡ 24 ሰዓት ሌት ተቀን በሦስት ፈረቃ ሲሠራ 11 ሰዎች ሞተውበታል፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ጽ/ቤት የድሮው ረዥሙ ሕንፃ ለአባዲና ፖሊስ ኮሌጅ የተሰጠ ሕንፃ ነበር፡፡ ጽ/ቤቱ የት ይሁን ተብሎ ሲፈለግ የድሮው ዓለም በቃኝ (ወህኒ ቤት) የነበረበት አጠገብ ያለው ሕንፃ ተመረጠ፡፡ ሌሎች ዙሪያውን ያሉት ከዚያ በኋላ የተሠሩ ናቸው፡፡

በዚያን ጊዜ የነበሩት ግዮን፣ ኢትዮጵያ፣ ራስ፣ ጣይቱ፣ ሒልተንና ገነት ሆቴሎች ብቻ ነበሩ፡፡ መሪዎቹ ሲመጡ የት ይረፉ ሲባል፣ በግዮን ሆቴል 32 መሪዎች የሚይዝ ቅጥያ ሁለት ፎቅ የተሠራው ያኔ ነው፡፡ ስብሰባው የተካሄደው አሁን ብሔራዊ ቤተመንግስት (ያኔ ኢዮቤልዩ ቤተ-መንግሥት) ተብሎ በሚጠራው ነበር፡፡ አዲስ አበባ አሸብርቃለች፡፡ በተለይ ከፒያሳ ማዘጋጃ ቤት እስከ ለገሃር ባቡር ጣቢያ ያለው ቸርችል ጐዳና፣ ከመስቀል አደባባይ እስከ ስድስት ኪሎ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ (ያኔ ገነተ - ልዑል ቤተመንግሥት) ድረስ በኢትዮጵያና በተለያዩ አገራት ባንዲራና መብራት አጊጦ ነበር፡፡ ዝግጅቱ ከተጠናቀቀ በኋላ መሪዎቹ የሚመጡበት ቀን ተቆረጠና ግንቦት 1955 ዓ.ም እንዲሆን ተወሰነ፡፡ የዝግጅቱ ዋና ተዋናይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ክቡር አቶ ከተማ ይፍሩ ነበሩ።

በወቅቱ ኃይለኛ ዝናብ ስለነበር ጃንሆይ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ እየተገኙ ሁሉንም መሪዎች የተቀበሉት በዣንጥላ ነው - ዝናብ እየዘነበባቸው፡፡ ቀይ ምንጣፍ ተነጥፎና ፖሊስ ባንድ ማርሽ እያሰማ፣ ለእያንዳንዱ መሪ 21 ጊዜ መድፍ እየተተኮሰ ነበር የተቀበሏቸው፡፡ በዚያን ጊዜ ትዝ የሚለኝ፣ የኮትዲቫር (ያኔ አይቮሪኮስት) መሪ የነበሩት ሁፌት ቧኜ በፍፁም በአውሮፕላን መጓዝ አይወዱም፡፡ ስለዚህ በመርከብ እስከ ጅቡቲ መጥተው ከዚያ ደግሞ በልዩ ባቡር ግንቦት 16 ቀን አዲስ አበባ ሲገቡ ደማቅ አቀባበል ተደርጐላቸዋል፡፡ በተወካይ የተሳተፉ አገሮች ቢኖሩም ኢትዮጵያን ጨምሮ 32 አገራት በመሪዎቻቸው አማካኝነት በስብሰባው ላይ ተሳትፈዋል፡፡ መሪዎቹና የልዑካን ቡድኑ አባላት አዲስ አበባ መግባት የጀመሩት ከግንቦት 13 ቀን ጀምሮ ሲሆን ተጠቃለው የገቡት ግንቦት 15 ቀን ነበር፡፡ ግንቦት 16 ቀን ምሽት ጃንሆይ በታላቁ ቤተመንግሥት በአፄ ምኒልክ አዳራሽ ለመሪዎቹ ክብር፤ ለልዑካን ቡድን አባላት፣ ለዲፕሎማቶች፣ ለጋዜጠኞች፣ በሀገር ውስጥ ላሉ መሳፍንት፣ ጳጳሳት፣ ሚኒስትሮች፣ መኮንኖች፣ ለታዋቂ ነጋዴዎችና ግለሰቦች በአጠቃላይ ከሦስት ሺም አምስት መቶ በላይ ለሚሆኑ እንግዶች ታላቅ የራት ግብዣ አደረጉ፡፡

ተጋባዦቹ ወደ አዳራሹ ከመግባታቸው በፊት በቤተመንግሥቱ ፊት ለፊት ባለው ሜዳ ላይ የተለያዩ ቀለማት ያላቸው ሪችት ተተኩሷል። አዳራሹ በአገር ባህል ቁሳቁሶች፣ የኢትዮጵያን ጥንታዊ ሥልጣኔ በሚያሳዩና በታዋቂ አርቲስቶች በተሣሉ ሥዕሎችና በኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓለማ አሸብርቋል፡፡ የክብር ዘበኛ፣ የጦር ሠራዊትና የፖሊስ ሠራዊት የሙዚቃ ቦንቦችም ልዩ ልዩ ጥዑመ ዜማዎችን በማቅረብ እንግዶቹን ሲያስደስቱ አምሽተዋል፡፡ ደቡብ አፍሪካዊቷ ማሪያ ማኬባ “የጥንቱ ትዝ አለኝ” የሚለውን የዶ/ር ጥላሁን ገሠሠን ዜማ ስታንቆረቁር ጭብጨባው ቀለጠ፡፡ ወደ አዳራሹ የተገባው ሁለት ለሁለት እጅ ተያይዞ ነበር፡፡ በመጀመሪያ የገቡት የኢትዮጵያ ንጉሥ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴና የግብፁ ፕሬዚዳንት ጋማል አብዱልናስር ነበሩ፡፡ ጃንሆይ አጭር እንደ መሆናቸው መጠን፣ እጅ ለእጅ ተያይዘው ሲገቡ ጭብጨባው ቀለጠ፡፡ በጣም ረዥም ከሚባሉት ጋማል አብድልናስር ሌሎችም በፊደል ተራቸው መሠረት ሁሉም መሪዎች እንዲገቡ ተደረገ፡፡

እራት ከተበላና ከተጠጣ በኋላ ክቡር ጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ ከፈረንሳዊት ሚስታቸው ጋር ወደ መድረክ በመውጣት ዳንስ አስጀምረዋል። በማግሥቱ ግንቦት 17 ቀን 1955 ዓ.ም 32ቱ መሪዎች ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍሪካን አንድነት ድርጅት ቻርተር በፊርማቸው አፀደቁ፡፡ ቻርተሩ ለም/ቤቱ ቀርቦ በሙሉ ድምፅ አፀደቅነው። ቻርተሩ ለፓርላማ የቀረበው፣ ዓለም አቀፍ ውሎችንና ስምምነቶችን ም/ቤቱ ማወቅ ስላለበትና በቻርተሩ አንቀጽ 23 መሠረት አባል አገሮች ለድርጅቱ በየዓመቱ የሚከፍሉትን መዋጮ በበጀት ተይዞ መፅጸቅ ስላለበት ነው፡፡ ክቡር ፊታውራሪ አበበ ሥዩም ግን ጥቂት ቅሬታ አላቸው፡፡

“ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ እንግሊዝኛ ፈረንሳይኛ ተናጋሪ በመጋል የተከፋፈሉትን የአፍሪካ መንግሥታት አስተባብረው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ቻርተር እንዲፈረም ያደረጉ ታላቅ መሪ ነበሩ፡፡ አሁን በአፍሪካ ኅብረት አዳራሽ ፊትለፊት የጋናው መሪ የክዋሜ ንኩሩማ ሐውልት ብቻ እንዲቆም በመደረጉ ቅሬታ አለኝ፡፡ ወደፊትም ቢሆን ለጃንሆይና ለመሥራች መሪዎች መታሰሲያ ሐውልት ይቆምላቸዋል የሚል እምነት አለኝ” ብለዋል፡፡ ሌላው ቅሬታቸው ደግሞ የአፍሪካ አንድነት ሲመሠረት የነበሩ ጥቂት የዓይን እማኞች ስላሉ እነሱ በአፍሪካ ኅብረት ምሥረታ 50ኛ ኢዮቤልዩ በዓል ላይ እንዲገኙ ያለመጋበዛቸው አሳዝኖአቸዋል፡፡

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ሰውየው መኪና እያሽከረከረ ነበር፡፡ አራትና አምስት ዓመት የሚሆነው ልጁን ኋላ መቀመጫ ላይ በመናው ቀበቶው አስሮ አስቀምጦታል፡፡ እናላችሁ ድንገት አንድ የትራፊክ ፖሊስ ያስቆመዋል፡፡ “ጌታዬ መንጃ ፍቃድ…” (ስሙኝማ…የሆነ ግራ የሚገባኝ ነገር አለ…በትራፊከ ፖሊስና በአሽከርካሪ መካከል ያለው መንጃ ፈቃድ የመጠየቅና ላለመስጠት የሚደረገው ክርክር ሶርያ ላይ የመሣሪያ ማዕቀብ ይጣል/አይጣል ከሚለው እሰጥ አገባ እኩል ጊዜ የሚወስደው ለምንድነው? የትራፊክ ፖሊስ ከአንድ አሽከርካሪ ጋር ሲከራከር አንዳንድ ጊዜ ሀይ ባይ እየጠፋ ትራፊኩ እንዴት እንደሚጨናነቅ ልብ ብላችሁልኛል!) “ምን አደረግሁ?” ሲል ሰውየው ይጠይቃል፡፡

የትራፊክ ፖሊሱም፣ “ሞባይል እያወሩ ሲሄዱ ነበር” ይለዋል፡፡ በዚህ ጊዜ ጸጉሩ ሊለወጥ ወደሚችልባቸው ቀለሞች ሁሉ ተለውጦ “እንትን ያላለበት ዳገት…” የሌለው ባለመኪናው “እኔ በጭራሽ በሞባይል አላወራሁም!” ብሎ ድርቅ ይላል፡፡ ድርቅ ማለት ብቻ ሳይሆን እንደውም “እንዴት እኔን የሚያክል ሰው እንዲህ ትደፍረኛለህ!” አይነት ቃና ነበረው አሉ፡፡ እናላችሁ…ትራፊክ ፖሊሱም “በዓይኔ በብረቱ አይቼዎት!” አይነት ክርክር ያደርጋል፡፡ ሰውየው ግን ጭራሽ የ‘ምኒታ ተቆጢታ’ አይነት ሆነ፡፡ “አይደለም በሞባይል ላወራ ሞባይሌንም ከቤት ይዤ አልወጣሁም…” ይላል፡፡ ይሄኔ ትራፊክ ፖሊሱ ግራ ይገባውና ሊለቀው ወስኖ “እሺ በሉ…” ምናምን ነገር ይላል፡፡ ይሄን ሁሉ ጊዜ ኋላ መቀመጫ ላይ የተቀመጠው ልጅ እየተወራጨ እሪታውን ያቀልጠዋል፡፡

አባቱ ዝም በል ቢለው ጭራሽ ባሰበት፡፡ ይሄኔ ትራፊክ ፖሊሱ እንደ ማባበል “ማሙሽ ምን ሆነህ ነው?” ይለዋል፡፡ ትንሹ ልጅ ምን ቢል ጥሩ ነው…“አባዬ በሞባይል መታኝ!” ለካስ ሰውየው ሞባይሉን ከትራፊክ ፖሊሱ ለመደበቅ ወደኋላ ሲወረውር ልጁን ቀውሮታል! እናላችሁ ዘንድሮ ነገርዬው “አባዬ በሞባይል መታኝ!” እየሆነ ነው፡፡ እናላችሁ…ምስጢር እየወሰዱ በመዘክዘክ ብዙ ወዳጅነቶች እየፈረሱ ነው፡፡ ታዲያላችሁ…በደህናው ጊዜ የሆድ የሆዳችሁን “እሱ ማለት እኔ ማለት ነኝ…” ብላችሁ ለሆነ ወዳጃችሁ ያወራችሁት ነገር ሁሉ…አለ አይደል… ለእናንተ ይወራላችኋል፡፡ እናማ…እንደ ‘አገር ጉዳይ’ በከፍተኛ ምስጢርነት ያወራችሁት ነገር…በሦስተኛው ቀን ዞሮ፣ ለእናንተው ይነገራችኋል፡፡

“ስማ ያቺ አጅሬ የሆነ ነገር ሠራችህ የሚሉት እውነት ነው?” “የት ሰማህ?” “ሰማኋ! የሆነ ሰው ምስጢር ብሎ የነገረኝ ነው።” እናላችሁ…አንዳንድ ጊዜ ምን የሚባል ነገር አለ መሰላችሁ…የሆነ ወሬ እንዲናፈስ ከፈለጋችሁ “ከፍተኛ ምስጢር ነው…” ብላችሁ አውሩ የሚሉት ነገር አለ፡፡ ደግሞ ዘንድሮ እንደዛ ‘የሚሸቱ’ መአት ነገሮች እየሰማንና እያነበብን ነው፡፡ እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ስለ ‘ምስጢር’ ካወራን ይቺን ስሙኝማ፡፡ የእራት ግብዣ ላይ ነው አሉ፡፡ ተጋባዦቹ ከወንዶችና ከሴቶች ይበልጥ ታማኝ ማን ነው በሚል ርዕስ ዙሪያ ነበር እየተከራከሩ የነበሩት፡፡ አንድ ሰውዬ በንቀት “አንዲቷም ሴት ምስጢር መጠበቅ አትችልም!” ሲል ተናገረ፡፡ ይሄኔ አንዲት ቆንጅዬ ሴት እንዲህ አለች፡፡ “ባልከው አልስማማም፡፡

ለምሳሌ እኔ ሃያ አንድ ዓመት ከሞላኝ ጀምሮ ዕድሜዬን በምስጢር ነው የያዝኩት፡፡” ሰውየውም “ምን አለ በዪኝ አንድ ቀን ትዘረግፊዋለሽ…” አላት፡፡ እሷ ምን ብላ ብትመልስ ጥሩ ነው… “በጭራሽ አልዘረግፈውም፡፡ አንዲት ሴት ለሀያ ሦስት ዓመት ምስጢር መያዝ ከቻለች ዕድሜ ልክ መያዝ ትችላለች ማለት ነው፡፡” አሪፍ አይደል.. ለክፉም ለደጉም ሃያ አንድ እና ሀያ ሦስት ይደመርልንና በ‘ሰርቲፋይድ’ የሂሳብ ባለሙያ ተረጋግጦ ይምጣልንማ! ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…አሁን፣ አሁን ‘ዜና’ ተብለው የሚወጡ ነገሮችን (በተለይ ‘ቦተሊካ—ተች’ የሆኑትን) ለመቀበል በጣም እየቸገረን ነው፡፡

እነ ‘ፌስቡክ’ የጥቅማቸውን ያሀል አንዳንዴ እኛንም ‘ጦጣ’ ለማድረግ የተመቹ እየሆኑ ነው፡፡ እናላችሁ…በሆነ ወገን አካባቢ ትንሽ “አደባለቀውና እርጥቡን ከደረቅ…” ቢጤ ለመፍጠር እንደ ሰበር ዜና ‘የሚረጩ’ ነገሮች በአጠቃላይ ‘ሶሻል ሚዲያው’ ላይ ብቻ ሳይሆን ‘ሜይንስትሪም ሚዲያ’ የሚሏቸው ላይ ያለንን እምነት እየሸረሸረብን ነው። እናላችሁ…አንዳንድ ዜናዎችን ሰምተን ወይም አንብበን “ይቺ ነገር ከእነእንትና የመጣች መሆን አለባት…” ለማለት እየተገደድን ነው፡፡ ልክ ነዋ…ዘንድሮ ጠርጥረን ከሚያመልጡን ነገሮች ይልቅ ሳንጠረጥር አደናቅፈው የሚጥሉን በዝተዋል፡፡ አባቶቻችን “ሽንብራውን ዘርተን እሸቱን ስንበላ አወይ የእኛ ነገር ሁልጊዜ ጥርጠራ” ያሉት ነገር ዘንድሮ ነው የምር እውነት የሆነው፡፡ እናላችሁ…ትንሽዬዋን ምስጢር እንኳን መነጋገር የማንችልበት ደረጃ ላይ መድረሳችን የምር አሳዛኝ ነው፡፡

ምስጢር የሚያካፍሉት ወዳጅን ያህል ‘ናቹራል ሬመዲ’ አልነበረማ! ‘ምስጢር’ ብላችሁ የተነጋገራችሁት ‘ምስጢር’ እየተባለ እንደ ቀለበት መንገድ ህዝቡ መሀል ሲሽከረከር አሪፍ አይደለም፡፡ ይቺን የ‘ምስጢር አጠባባቅ’ ስሙልኝማ… “ለእሷ እንዳትነግራት ያልኩህን ምስጢር እንደነገርካት ነገረችኝ፡፡” “እንደነገርኳት እንዳትነግርህ ነግሬያት ነበር፡፡” “እንግዲያው እሷ እንደነገረችኝ ለአንተ መንገሬን እንዳትነግራት፡፡” እና…እንዲህ ሆኖላችኋል፡፡ ይቺን ከሆነ መጽሔት ቢጤ ነገር ያገኘኋትን ስሙኝማ…አቶ ባል ለጓደኛው እንዲህ ይለዋል፡፡ “ጎረቤቶቻችን የምንጋገረውን እንዳይሰሙ ሚስቴ የሬድዮኑን ድምጽ በሰፊው ትለቀዋለች፡፡” ጓደኝዬውም “እና እንዳሰበችው ሆነላት?” ሲል ይጠይቃል፡፡ “እንዳሰበችውም፣ እንዳላሰበችውም ሆነ፡፡”

“ምን ማለት ነው?” “ጎረቤቶቻችን እኛ የምንለውን አይሰሙም። ችግሩ እነሱ የሚሉትን እሷም እንዳትሰማ ድምጹ ከለከላት፡፡” ማርክ ትዌይን የሚባለው አሜሪካዊ ደራሲ እንዲህ ብሏል አሉ፡፡ “ሁሉም ሰው እንደ ጨረቃ ነው፡፡ ለማንም የማያሳየው ጨለማ ወገን አለው፡፡” ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…‘የስኬታማ ትዳር ምስጢሮች’ ተብለው የሆነ ድረ ገጽ ላይ የለጠፏትን የሆነ ባል የተናገረውን አንብቡልኝማ! እኔና ሚስቴ መልካም ትዳራችንን ለማቆየት የራሳችን ምስጢሮች አሉን፡፡

1) በሳምንት ሁለት ጊዜ ጥሩ ሬስቱራንት ሄደን ጥሩ ምግብ እንበላለን፣ ጥሩ ወይን እንጠጣለን ከሰው ጋርም እንቀላቀላለን። እናም… እሷ ማክሰኞ ቀን ትሄዳለች እኔ ደግሞ ዓርብ ቀን እሄዳለሁ፡፡

2) ደግሞም በተለያዩ አልጋዎቸ እንተኛለን— እሷ ፍሎሪዳ ትተኛለች፣ እኔ ኒው ዮርክ እተኛለሁ፡፡

3) እኔ ሚስቴን ሁሉም ቦታ እወስዳታለሁ፣ እሷ ግን ከሁሉም ቦታ እኔ ሳላስፈልጋት በራሷ ተመልሳ መምጣት ትችላለች፡

4) ሚስቴን “ለትዳራችን ዓመታዊ መታሰቢያ የት መሄድ ትፈልጊያለሽ?” ብዬ ጠየቅኋት፡፡ እሷም “ለረጅም ጊዜ አይቼው የማላወቀው ቦታ” አለችኝ። እኔም “ማብሰያ ቤት ቢሆን ምን ይመስለሻል?” አልኳት፡፡

5) ሁልጊዜ እጅ ለእጅ እንያያዛለን፡፡ እጇን ከለቀቅኋት የሆነ ነገር ትገዛለች፡፡ እናላችሁ…የግልና እዛው በእዛው መቅረት ያለበት ምስጢር ሁሉ እየተበተነ አይደለም ሌላውን ራሳችንን መጠርጠር ልንጀምር ምንም አልቀረን። ሰውየው ምን አለ አሉ መሳላችሁ…“ሁሉም ሰው ሲያወራው ምስጢር መሆኑን አወቅሁ፡፡” “አባዬ በሞባይል መታኝ!” አይነት ነገር አሪፍ አይደለም፡፡ ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል