Saturday, 08 June 2013 08:19

አዝናኝ ትዝታ

አስገራሚ ሠርግ በ50ኛው ዓመት የአፍሪካ ህብረት ክብረ - በዓል ጉያ
በወርሃ ግንቦት፤ በ24ኛው ቀን፤ በ2005 ዓ.ም፤ አምስት ኪሎ ድህረ ምረቃ አዳራሽ የተፈፀመ የሰርግ ገጠመኝ ነበር የጽሑፌ መነሻ፡፡ ከዚያ በፊት ግን በቀጥታ ወደ “ገደለው” ሳንዘልቅ መግቢያ ነገር እናብጅ፡፡
ሠርግ የደስታውን ያህል ጣጣው ብዙ ነው፤ በየሠርጉ ውስጥ ብዙ ጉድ አለ፡፡ ሚዜዎቹ የጠፉበት ሠርግ ብዙ ነው፡፡ ሙሽሪትና ሙሽራው ተጣልተው የጠርሙስና የብርጭቆ መወራወር የተከሰተበት ቀውጢ ሠርግ ነበር፡፡ ድንኳን ላያቸው ላይ የወደቀባቸው ሙሽሮች፤ ነብሰ-ጡር ሙሽሪት ፍስስ ልፍስፍስ ብላ (fainting) የወደቀችበት ወዘተ. ብዙ አስደንጋጭ ገጠመኞች ታይተዋል፡፡ ዛሬ ደግሞ አዝናኝ ናቸው ያልኳቸውን ጥቂት አጋጣሚዎች በየመልኩ ላቋድሳችሁ፡፡

የሰላም እርግብ ሰላም አጣች!
በአንድ ራሰ በራ፤ ፀጉሩ በጂሌት ምላጭ ሳይሆን በፕላስተር የተነሳ የሚመስል፤ ሙሽራ ሰርግ ላይ፣ አናቱ ላይ የሆነች እርግብ ለማስቀመጥ የመጡ አስተናጋጆች፤ በላብ የወዛው የሙሽራው ትኩስ መላጣ እያዳለጣት በሰላም መቆም ባለመቻሏ በጥፍሯ ቆንጥጣ ለመቆም በምታደርገው ጥረት ህመሙ የበረታበት ሙሽራ፣ በሰርጉ ቀን ለቅሶ ለቅሶ ሲለው ታይቷል፡፡

የእነቶሎ ቶሎ ቤት - ግድግዳው ሰንበሌጥ!
በሆነ ሰርግ ላይ ደግሞ ጥንዶቹ ኬክ ለመቁረስ የቆሙበት መድረክ በአልባሌ ብረት የተሰራ ሳንቃ ኖሮ ደልደል ያሉት ሙሽሪትና ሙሽራው ገና ሲቆሙበት ከእነ ኬካቸው ተከንብለው አፈር ቅመው ተነሱ፡፡ ከሁሉ በላይ ግን አስደምሞኝ የነበረው የቪዲዮ ባለሙያው፣ ምንም ድንጋጤ ሳይስተዋልበት ሚዜዎችና እንግዶች ሙሽሪትና ሙሽራውን ለማንሳት ሲያደርጉት የነበረውን ርኩቻ አንድ ሳይቀረው ሪከርድ አድርጐ ማኖሩ ነበር፡፡

“በገዛ ዳቦዬ ልብ ልቡን አጣሁት!”
በአንድ የሰርግ ስነስርአት ላይ ደግሞ የተጠራው እድምተኛና አዳራሹ የማይመጣጠን ሆኖ ወንበር ያጣ እንግዳ መተላለፊያው ላይ ተደርድሮ በመቆሙ ሙሽሮች ምግብ ለማንሳት መተላለፊያ አጡ፡፡ ፊታቸው ጠቆረ፡፡ እንግዶቹ ከሙሽሪትና ሙሽራው ትይዩ ቆመው በልባቸው “እናንተ ብሎ ጠሪ፤ እኛ ብሎ እድምተኞች” ያሉ መሰሉ በሆዳቸው፡፡

“ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ!”
አንድ ጊዜ ደግሞ ጊዮን ሆቴል መናፈሻ ላይ በነበረ የፎቶ ፕሮግራም ከሞቅታም አልፎ ወደ ስካር የገቡ የሚመስሉ ዲያስፖራ ሙሽሪትና ሙሽራ፣ የሚዜና የአጃቢ ነገር ቁብ ሳይሰጣቸው እንዴት ከልባቸው ሲጨማጨሙ፣ ሥር-የሰደደ ስሞሽ (deep-kiss) ደረጃ ሲደርሱ ታዩ፡፡ ቀድሞ ነገርስ “በዚያች ቀን ያልታበደ መቼ ይታበዳል?” ያሉ ይመስላሉ፡፡ ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ!!
ለጊዜው የእኔ ገጠመኞችን እዚህ ላይ ገታ አድርገን ከእኔ በተሻለ ሊያዝናኑ የሚችሉ ትዝታዎችን እንደሚያስታውሱአችሁ ግን ተማምነን ወደ ዛሬው ጽሑፍ ልውሰዳችሁ፡፡
50ኛው የአፍሪካ ህብረት በአሉታ ወይም በአዎንታ ጥሎት የሄደው ትዝታ ለመኖሩ ጥርጥር የለውም፡፡ መንገዶች እየተዘጉ ስንቱን ፀጉር አስነጭተዋል፡፡ አሁን የተከፈተው መንገድ ከአንድ ማስታወቂያ ቆይታ በኋላ እንመለሳለን የተባለ ይመስል ይዘጋል፡፡ ቤቶች ለ50ኛው መንገድ ሲባል ፈርሰዋል - ሆኖም አሪፍ አሪፍ መንገድ አግኝተናል፤ “ፈጣን ልማት” አይተናል፡፡ ዱሮ ለማኞች ይታፈሱና እሥር ቤት ይታጐሩ ነበር፣ ቆሻሻ በአሮጌ ቆርቆሮ አጥር ይከለል ነበር፡፡ (በአአድ ሰሞን)…ወዘተ
ለነገሩ እንደ እኔ እምነት የድህረ ምረቃው አዳራሽ ገጠመኝ ከአዝናኝነቱ ባለፈም ታሪካዊ ፋይዳው የሚጐላ መስሎ ይሰማኛል፡፡ በመሆኑም ይህን የአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት ክብረ በአል በተከበረበት ሳምንት የተደገሰው ሰርጋቸውን አስታክኮ የሙሽሪትና የሙሽራው ዘለአለማዊ ዝክር በሚሆነው በቪዲዮና በፎቶ ታሪካዊ ማስታወሻ ለማኖር ሃሳቡን ያፈለቀውንና በተግባር ያዋለውን ግለሰብ ሳላደንቅ አላልፍም፡፡
ጥንዶቹ እንደ ቀደሙት አባትና እናቶቻችን ሙሽራዎች እፍረትና መሽኮርመም የማያውቃቸው ስለነበሩ ወደ አዳራሹ በመጡባት ክፍት ዳፕ መኪና ህዝበ አዳምን በየአደባባዩና በየመንገዱ ሰላም እያሉና እየደነሱ፣ ከዚያም ከመኪና ወርደው ወደ አዳራሹ ባደረጉት ጉዞ ዘና፤ ፈታ ብለው እየጨፈሩ የሚጓዙ ዓይነት ናቸው፡፡
የምግብ መስተንግዶና፤ ጭፈራው፤ ሌላም ሌላም ፕሮግራም በአዳራሹ ውስጥ ተካሄደ፡፡ ከዛም ዲጄው “የኬክ መቁረስ ስነ ስርአት ከአዳራሹ ውጭ በክፍት አየር ላይ ይካሄዳል” ሲል አወጀ፡፡
“ከአዳራሽ ውጭ ኬክ ቆረሳ ምን ሊፈይድ ይሆን?” ሳልል አልቀረሁም፡፡ የሆነው ሆኖ ዲጄውም ማጫወቻዎቹን አዘጋጀ፤ የፎቶና የቪዲዮ ባለሙያዎች መብራቶቻቸውን አምቦግቡገው ካሜራዎቻቸውን ወድረው በመጠባበቅ ጀመሩ። ኬክ አዘጋጆች ኬካቸውን አዘጋጅተው ሲቀርቡ የሁሉም እድምተኛ ትኩረት ኬኩ ላይ ሆነ፡፡ በሚገርም ሁኔታ ኬኩ በአፍሪካ ካርታ ቅርጽ የተሰራ ሆኖ ሙሉ በሙሉ በአረንጓዴ፤ ቢጫና ቀይ ቀለም የተዋበ ሲሆን ዙሪያውን ቁራጭ ኬኮች ተዘጋጅተው የሃምሳ ሁለቱ (52ቱ) የአፍሪካ ሀገራት ባንዲራ ተሰክቶባቸዋል፡፡ አስደማሚ ትእይንት ነበር!!
ሙሽሪትና ሙሽራው ወደ መድረኩ ለመውጣት ሲዘጋጁ ዲጄው፤ ቀዳማዊ ኃ/ስላሴ በአፍሪካ ህብረት ስብሰባ ካቀረቡት ንግግር በፊቸሪንግ በማስገባት፣ በቀጣይም አፍሪካ ነክ ሙዚቃዎችን በማከታተል ካሰማ በኋላ የኢትዮጵያን ህዝብ መዝሙር ለቀቀ፡፡ ሁለቱ ሙሽሮች ወታደራዊ ሰላምታ እንደሚያቀርብ ወታደር በተጠንቀቅ ቆመው መዝሙሩ ተዘመረ። ከዛም ባንዲራ የተሰካበትን ኬክ ተራ በተራ እንድንወስድ ተደርጐ ሁላችንም እጆቻችንን ወደ ላይ ከፍ በማድረግ በአፍሪካ ሙዚቃዎች ጭፈራና ዳንስ ተከተለ፡፡

ታሪካዊ ፋይዳው
…እስቲ በምናብ መርከብ 50 ዓመታት ወደፊት እንቅዘፍና እ.ኤ.አ 2063 ላይ ደርሰናል እንበል። አፍሪካ እንደ ምኞቷ አንድ የመሆን ህልሟ ተሳክቶ በአንድ የገንዘብ ኖት፤ በአንድ የኢኮኖሚ ፖሊሲና በመሳሰሉት ጉዳዮች መጠቀም ጀምራለች። ኢትዮጵያም ድህነትን ታሪክ አድርጋ የላቀ የኢኮኖሚ እድገት ተቀዳጅታለች፡፡ እንዲሁም የአፍሪካ መዲና መቀመጫ በመሆኗ ለህብረቱ ያላት አስተዋጽኦ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ የዛሬዎቹ ሙሽራዎች ቢያንስ የ80 አመት አዛውንት ይሆናሉ፤ ካደላቸውም አባት እልፍ ሲልም አያት ሆነው ይህን ፊልም ከልጅና ልጅ ልጆቻቸው ጋር ይመለከቱታል። ያኔ የዛሬው ትውልድ ከባለፉት ትውልድ የሃገር ፍቅርንም ሆነ ፓን አፍሪካኒዝምን ለቀጣይ ትውልድ ለማስተላለፍ ሲያካሂድ የነበረውን ትግል ጐልቶ የሚያሳይ ይሆናል፡፡ የዚያን ዘመን ተረካቢ ትውልድም ይማርበታል ብዬ አምናለሁ፡፡
የሙሽሮቹ ቤተሰብና መጻኢ ልጆቻቸው ይቅርና እኔ የዚህን ጽሑፍ አቅራቢና ሌሎች ካሜራና ሞባይላቸውን አውጥተው ታሪክ ለማስቀረት ሲጣደፉ የነበሩ እድምተኞችን ያስደመመው ይህ ትዕይንት ዘመን አልፎ ዘመን ሲተካ የጥቁር አፍሪካዊ ስሜትን አጉልቶ ያሳያል። ታዲያ ከዚህ በላይ ምን ድል አለ?

እንደመሰናበቻ
ያው የአፍሪካ ባንዲራ የተሰካበት ኬክ ሲከፋፈል፤
እኔ ለኬክ ቆራሹ፡ “ለእኔ የደረሰኝ ኬክ ባንዲራ የማን ሀገር ይሆን?”
ኬክ ቆራሹ፡ “የአፍጋኒስታን” አለኝ፤ ኬኩን ወደ እጄ እያቀበለ፡፡
ቸር ሰንብቱ!!!

Published in ህብረተሰብ

አንድ ሰሞን ‘እምብርትዬዋ’ ታየች ብለን “እሪ!” እንዳላልን… ይኸው “ኽረ እምብርት ምን አላት፡ ሺህ ጊዜ ትታይ!” የምንልበት ጊዜ መጣ! እንዴት ሰነበታችሁሳ!

ሰኔ ግም አለ አይደል! ‘በሰኔ ካልዘሩ በጥቅምት ካለቀሙ እህል አይገኝ ከድንበር ቢቆሙ፣’ ይላሉ የጥንት ሰዎች፡፡ ልጄ…እንደ ምንም ‘መሥራት እስከተቻለ’ ድረስ በሰኔ ለመዝራት መሞከር ነው፡፡ እንቅስቃሴው ሁሉ የሆነ የአርክቲክ በረዶ መጥቶ የተዘረገፈበት ይመስል ቀዝቅዟል ይላሉ፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…የአፍሪካ ህብረትን ‘ጎልደን ጁብሊ’ን አከበርን አይደል! እሰይ…እንኳን በሰላም መጥተው በሰላም ሄዱማ! በእንግዳ ተቀባይነታችን ‘ወዛም ወዛሞቹ’ በሚያልፉባቸው መንገዶች ‘ዝር ማለት’ ትተን፣ አብዛኞቻችን በቺቺኒያና በቦሌ መድሀኔዓለም አካባቢ ካሉ መዝናኛዎች ባንታመምም እንደታመመ ‘ሲክ ሊቭ’ ወስደን፣ በሆቴሎች በር ላይ ተብጠርጥረን እየተፈተሽን… አስተናግደናል፡፡

እናላችሁ…ያው በእንግዳ ተቀባይነታችን የእኛን ጠማማ ጭልፋና ቀዳዳ ትሪ ደብቀን ለእንግዳ የምናስቀምጠውን አብለጭላጭ ጭልፋና ሊነኩት የሚያሳሳ አውጥተን በዛ ሰሞን ‘እንግዶቻችንን ስናስተናግድ’ የአዲስ አበባ እንትናዬዎች የስንት ዓመታቸውን ዘጉ አሉ! (ወላ ‘ዶላር’፣ ወላ ‘ዩሮ’፣ ወላ ‘ፓውንድ’ ፈሰሰ አሉ!) እኔ የምለው… እንግዲህ ጨዋታም አይደል …ልጄ ስንት አይነት ‘ኢንቪዚብል’ ቱሪዝም አለ መሰላችሁ! እናንተ የቲማቲም ዋጋ እንዲህ እንደ ወዳጃችሁ ‘ብለድ ፐሬዠር’ በአንዴ ሽቅብ ስለተወረወረበት ምክንያት ስትመራመሩ…በዚቹ በእኛዋ ሸገር ስንት ነገር ይካሄድባታል መሰላችሁ! (እግረ መንገዴን የሆነ ነገር ትዝ አለኝማ…ሰሞኑን የ‘ብለድ ፕሬዠር’ ነገርዬው ተባብሷል ያልከኝ ወዳጄ…ምኞትህን ነው የነገርከኝ ወይስ… መረጃው ከየት ተገኘ!) እናላችሁ…በፊት እንትን ሰፈር እንትን ቀበሌ ብለን የምናወራላቸው እንትናዬዎቹ ሔዋን ‘እጸ በለሱን ከመብላቷ በፊት’ እንደነበረችው ሆነው የሚደንሱባቸው ቤቶች…አሁን በየሰፈሩ ፈልተዋል ነው የሚባለው፡፡ ደግሞላችሁ…የእንትን ሰፈር የሦስት ብር ከሀምሳ ብር ሻይ ከስኒዋ በስተቀር ምኗም ሳይቀየር አሥራ ምናምን ብር የሚሸጥባት ሰፈር ብቻ ሳይሆን…ገና ‘ስቶን ኤጅ’ ውስጥ ናቸው የሚባሉት ሰፈሮች ሁሉ ‘መለመላችንን’ ሆነን የምንደንስባቸው ቤቶች ብዛት…አለ አይደል… ልክ እንደ ‘ምናምን ኤክስቴንሽን’ የተበተኑ ሊመስሉ ምንም ያህል አልቀረም፡፡ ምን ችግር አለ መሰላችሁ…አሁን አሁንማ ነገሮች በጣም የተለዩ እየሆኑብን ለመገረምም፣ ለመደነቅም ‘መተንፈሻ’ እያጣን ነው፡፡

መስከረም ላይ ራሳችንን ይዘን “ጉድ! ጉድ!” ያልንበት ነገር…ህዳር ላይ ብዙ ዓመት አብሮን የኖረ ይመስል ትከሻችን ሸከሙን ይለምደዋል፡፡ (‘ሌሎች ሸክሞችን እንደቻለው’ የሚለውን ማስከተል ይቻላል፡፡) ስሙኝማ…ካነሳነው አይቀር እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ሚዲያው ላይ አልፎ፣ አልፎ እነዚህ አይነት ችግሮች ‘እግረ መንገድ’ ጠቀስ ተደርገው ቢያልፉም…ብዙ ጊዜ.. አለ አይደል…የሩኒን ቁርጭምጭሚት ያህል እንኳን… የአየር ሰዓት ሲሄዱ አይታዩም፡፡ ታዲያላችሁ…የዘንድሮ የእንትናዬዎቻችን አለባባስ ለየት ብሎ ነበር አሉ፡፡ (ልክ ነዋ… “ለሀምሳኛ ዓመት ያልሆነ….ዳዋ ይምታው!” የተባለ ይመስል ነበር!) አለ አይደል…እንዴት ነበር አሉ መሰላችሁ…ካፖርት ይለበሳል፣ ከዛ ስር የ‘ብሬስት’ መያዣና ‘ግለገል’ ሱሪ ብቻ! አራት ነጥብ! (እናማ…ይህ ሁሉ በማታ ሳይሆን በጠራራው ጸሀይ እንደሆነ ልብ በሉልኝማ! አሁንማ…ዋናው ቦሌ በያዝ ለቀቅም ተከፈተ አይደል…ለሌሎች ‘ጉዶች’ መዘጋጀት ነው!) እናላችሁ…ይሄ የሆነው እዚቹ እኛዋ ስልጣኔዋ ‘አናቷ ላይ የወጣባት’ ከተማችን ውስጥ ነው! (ወይም…ስልጣኔ አዲስና አገር በቀል ‘ዴፊኒሽን’ ያገኘባት የምትመስል ከተማ ውስጥ!) ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ለከርሞ ደግሞ (‘ለከርሞ’ የሚለው ከአንድ ወር እስከ አንድ ዓመት መሆኑ ይመዝገብልን!) ከቀሩት ሁለቱ ነገርዬዎች አንደኛዋ ትጣልና…ካፖርትየውም ርዝመቱ በግማሽ ሊያጥር ይችላል፡፡

አንድ ሰሞን ‘እምብርትዬዋ’ ታየች ብለን “እሪ!” እንዳላልን…ይኸው “ኽረ እምብርት ምን አላት፡ ሺህ ጊዜ ትታይ!” የምንልበት ጊዜ መጣ! እናላችሁ…የዛ ሰሞኑ “ከካፖርት ስር ግልገል ሱሪ…” ዝም ብሎ የመጣ አይደለም፡፡ የእኛዋ ከተማ የስልጣኔ ‘ዝግመተ ለውጥ’ ያመጣው ነው፡፡ ቂ…ቂ… ሀሳብ አለን…“ወዴት እየሄድን ነው?” የሚለው ጥያቄ (“ምን አይነት አገር እየሆንን ነው?” እንዳልል የኮፒራይት ጥያቄ ያስነሳብኛል ብዬ ነው፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…) የጠቃሚነቱ ዘመን ያበቃለት መሆኑን የሚገልጽ የሆነ መመሪያ ምናምን ነገር ይውጣልንማ።

እኛ የምንሄድበት ቦታ በቃ…ሌላው የሰው ልጅ ያልደረሰበት ቦታ ነዋ! ልክ ነዋ…ምን መሰላችሁ… እኛ ስልጣኔያችን ከምንም ተነስቶ አራትና ከዛ በላይ ዲጂት ዕድገት ማስመዝገቡን ለማየት…አለ አይደል…መንገዶቻቸው በሰፉ፣ ህንጻዎቻቻው በረዘሙ፣ አብዛኞቹ የሚዝናኑባቸው ደንበኛዎቻቸው የሚይዙት የሚጨብጡትን ባሳጣቸው፣ የአንድ ምግብ ዋጋቸው ለፒያሳና ለጉለሌ የወር በጀት በሆነባቸው አካባቢዎች ብቅ ማለት ይበቃል፡፡ እናማ…“ከካፖርት ስር ግለገል ሱሪ…” ዝም ብሎ የመጣ ነገር ሳይሆን የደረስንበት የስልጣኔ ደረጃ ማስመስከሪያ ነው! ነገርዬው…‘ውሀ ለሚወስደው ሰው በትርህን እንጂ እጅህን አትስጠው’ ነው፡፡ እናማ…አንዳንድ ነገሮችን ስታዩ ‘ውሀ እየወሰደን’ ያለን መአት ሰዎች ነን፡ ችግሩ ምን መሰላችሁ…ውሀ ውስጥም ሆነን፣ የውሀውም ከፈታም እየጨመረ…ደረቅ መሬት ላይ ያለን የሚመስለን እየበዛን ነው፡፡ የፉክክር አገር ሆኖላችኋል…አለ አይደል…እንትና ያደረገውን እንትና በማግስቱ ካላደረገ ‘የምጽአት ቀን መጣች’ አይነት ነገር ሆኗል፡፡ አያችሁልኝ ወይ ይህን አይነት ግፍ ተጉዘን ተጉዘን ስንደርስ አፋፍ እኔ ሴቷ ቆሜ ወንዱ ደክሞት ሲያርፍ፣ አሉ የድሮ እናቶቻችንና እህቶቻችን፡፡

እናላችሁ ዘንድሮ ደግሞ እንትናዬዎቹ ነገርዬአቸውን “ከካፖርት ስር ግለገል ሱሪ…” ሆኖ በ‘ስልጣኔ መርሸው’ ፕሬሚየር ሊግ ሲደርሱ…አለ አይደል… ወንድዬው ገና ሦስተኛ ዲቪዥን ሆኖ ‘ሱሪ ዝቅ’ ላይ ነው! ስሙኝማ…‘ሱሪ ዝቅ’ ነገር በጣም፣ በጣም…አለ አይደል…“ምን ይሻለን ይሆን?” የሚባል ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ የታክሲ ረዳቱም መካኒኩም…‘ሱሪ ዝቅ’ እየሆነ ስታዩ ዛሬን ሳይሆን ነገን ትፈሩታላችሁ፡፡ እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… ይሄ የግብጽ ነገርዬው እንዴት ነው? ታሪክ ራሱን አይደግምም…ምናምን ያለው ማነው? አሀ…መጠየቅ አለብና! ሲዶልቱብን በስውር ቪዲዮ ተቀረጹ ነው ምናምን የተባሉት…የፈርኦን አገር ባለስልጣኖች የምር ከአንጀታቸው ነው እንዴ! እናማ…ሰኔም ግም አለ…የወጣም ወጣ፣ የወጣም ‘እንዳልወጣ ሆነ’…የወጣም ‘ገባ’…ብቻ የወጣ እንደወጣ የሚቀረው ‘አማሪካን’ ምናምን ብቻ ሆኗል፡፡

ልጄ…የተወጣበት መሰላል ነቅነቅ ያለ እንደሆን አንደኛውን ስቦ ለመጣል ያለው ግፊያ ከቡናና ጊዮርጊስ ‘ደርቢ’ ካለው ግፊያ የባሰ እየሆነ ነው፡፡ አለ አይደለም…“መቼ በወደቀና እንደ ረግቢ ስፖርት ተጫዋቾች ላዩ ላይ በተከመርንበት…” ምናምን እያልን የምንጸልይ ነው የሚመስለው፡፡ እናላችሁ….ዘንድሮ ስንት ነገር እየሆነ፣…ለታሪክ አስቀምጦን እየታዘብን ነው፡፡ እንዴት ያለው ሩቅ ጭንቅ ያለው መንገድ አሻቅቦ ወጥቶ ወደ ታች መውረድ አሉ አባቶች…ወይ ሲወጡ መሰላሉ እንዳይነቃነቅ ጠለቅ አድርጎ ‘መቅበር’…ወይም ‘መውደቅ’ የማይቀር ከሆነ ህመሙ እንዳይሰማ ጂም መግባት! ቂ…ቂ…ቂ… (እነ እንትና ‘ጂም’ የተባለው ‘ወተር ማትረስ’ የሚሉት ‘የጭድ ፍራሽ ጠላት’ ላይ የሚደረገውን የ‘ሆሊዉድ ስተንት’ የሚመለከት እንዳልሆነ ልብ ይባልማ!) እናላችሁ…“ከካፖርት ስር ግልገል ሱሪ…” ጦስ ውጤቱ አሁን ሳይሆን እየቆየ ትውልድ ላይ እንደ ጥላ ተተክሎ አልለቅ እንዳይል አንድዬ ተአምሩን ያምጣልንማ! ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

የምድር አውሬ ሁሉ መነገጃና መሰባሰቢያ አንድ ገበያ ነበር ይባላል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አውሬ ሁሉ እገበያ ሲውል፤ አያ ጅቦ ቀርቶ ኖሯል፡፡ ማታ ሁሉም ከገበያ ሲመለስ ከጎሬው ብቅ ይልና መንገድ ዳር ይቀመጣል፡፡ ዝንጀሮ ስትመለስ ያገኛትና ገበያው እንዴት እንደዋለ ይጠይቃታል፡፡ “እቸኩላለሁ ጦጢት ከኋላ አለችልህ እሷን ጠይቃት” ብላው ሄደች፡፡ ጦጢት ስትመለስ ጠብቆ “ገበያው እንዴት ዋለ?” አላት፡፡ “መሽቶብኛል፡፡ ገና ብዙ ሥራ አለብኝ” ብላው አለፈች፡፡ ቀጥላ ሚዳቋ መጣች፡፡ ያንኑ ጥያቄ ጠየቃት፡፡ “እንኮዬ አህይት እኋላ አለች - እሷን ጠይቅ!! እኔ እነዝንጀሮ ቀድመውኛል፤ ልድረስባቸው” ብላው ሄደች፡፡ አህያ ስትንቀረደድ መጣች፡፡ ገበያው እንዴት እንደዋለ ጠየቃት፡፡ “ቆይ አረፍ ብዬ ላውራልህ” ብላ አጠገቡ ተቀመጠች፡፡

“ይሄ ተገዛ! ያ ተሸጠ!” ስትለው አመሸች፡፡ አያ ጅቦ ቀጠለና “ለመሆኑ እኔ እምዘለውን መዝለል ትችያለሽ?” አላት፡፡ “አሳምሬ” አለችው፡፡ እሱ የሞት ሞቱን ዘለለ፡፡ እሷ ግን እዘላለሁ ብላ ገደሉ ውስጥ ወደቀች፡፡ አያ ጅቦ ወርዶ ሆዷ ዘንጥሎ መብላት ጀመረ፡፡ እመት ውሻ በዛ ስታልፍ ስጋ ሸቷት መጣች፡፡ “ነይ ውረጂና እየመተርሽ አብይኝ” አላት፡፡ ወርዳ እየመተረች ስታበላው የአህያዋን ልብ አገኘችና እሱ ሳያያት ዋጥ ስልቅጥ አደረገችው፡፡ ቆይቶ “አንቺ ልቧ የታል?” ሲል ጠየቃት፡፡ ውሺትም፤ “ልብ ባይኖራት ነው እንጂ ልብ ቢኖራት መቼ ካንተ ዘንድ መጥታ ትቀመጥ ነበር?!” አለችው፡፡ “ታመጪ እንደሁ አምጪ፤ አለዛ አንቺንም እበላሻለሁ!” አለ፡፡ “አያ ጅቦ፤ ያለ ቂቤ? ያለ ድልህ? ደረቁን ልትበላኝ?” “ቅቤና ድልሁ ከየት ይመጣል?” አለ ጅቦ በመጎምጀት፡፡

“ከእመቤቴና ከጌታዬ ቤት አመጣለሁ” “ሄደሽ የጠፋሽ እንደሆን ማ ብዬ እጠራሻለሁ?” “እንኮዬ -ልብ- አጥቼ” ብለህ ጥራኝ፡፡ “በይ እንግዲያው ሄደሽ አምጪ” ብሎ ላካት፡፡ ቅርት አለች፡፡ ሲቸግረው “ኧረ እንኮዬ ልብ አጥቼ?” ሲል ጮሆ ተጣራ፡፡ ውሻም፤ “ከጌታዬና ከእመቤቴ ቤት ለምን ወጥቼ!” አለችው፡፡ ከዚያም የስድብ መዓት ታወርድበት ጀመር፡፡ ጅቦም፤ “አንቺም እጉድፍ እኔም እጉድፍ፡፡ አገኝሻለሁ ስንተላለፍ” አላት፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ውነትም ጉድፍ ስትለቃቅም አገኛት፡፡ ዐይኗ ፈጠጠ፡፡ “ዐይንሽ እንዴት እንዲህ አማረልሽ?” ሲል ጠየቃት፡፡ “በዐሥር የአጋም እሾክ ተነቅሼ!” አለችው፡፡ “እስቲ እኔንም ንቀሺኝ?” ተስማምታ ከጌታዋ አጥር ዓሥር የአጋም እሾህ ሰብራ አምጥታ ዐይኖቹን ቸከቸከችው፡፡ “ኧረ አመመኝ” ሲል፤ “ዝም በል ሲያጌጡ ይመላለጡ ነው፣ ማማር እንዲያው ይገኝ መሰለህ?” ትለዋለች፡፡ ሁለቱንም ዐይኖቹን አጥፍታ፤ “በል ና ሠንጋ ጥለው የሚሻሙ ጅቦች ጋ ልቀላቅልህ” ብላ፤ ውቂያ ላይ ያሉ ገበሬዎች ማህል ከተተችው፡፡ ወስዳ ጤፍ መውቂያ ሙጫቸውን እየመዘዙ ሊገድሉት ያራውጡት ጀመር፡፡ ውሻ ሆዬ እነሱ ሲሯሯጡ ዳቧቸውን ይዛ ወደቤቷ መጭ አለች!!

                                                           * * *

ያሰቡትን ቸል ሳይሉ ከፍፃሜ ማድረስ አስተዋይነት ነው፡፡ ያለኩያ ጓደኛ መያዝ፤ ነገርን ሳያመዛዝኑ ፈጥኖ አምኖ መቀበል ከጥቃት የሚያደርስ ቂልነት ነው፡፡ አታላይ ለጊዜው የመብለጥለጥ ምኞቱን ቢያረካም፣ የፈፀመው ደባ እንደሚደርስበት የዥቡን አወዳደቅ ማስተዋል በቂ ነው! ብልህ በዘዴ ከአደጋ ያመልጣል፡፡ ኃይለኛ የሆነ ጠላት ቢገጥመው እንኳ በጥበብ ለመርታት ይችላል፡፡ ሀገራችን ያለችበት ሁኔታ አሳሳቢ ነው፡፡ አንዱ ሲሠራ ሌላው ሲያፈርስ፣ አንዱ ሲታሰር ሌላው ሲተበተብ፤ የሁኔታዎች መወሳሰብ ይከሰታል፡፡ ከውስብስቡ ሁኔታ ለመውጣት እጅግ አስፈላጊው ነገር ትዕግሥትና ስክነት ነው፡፡ ባላንጣ፤ ሀገር ያልተረጋጋበትን ሰዓት መምረጡ የታወቀ ጉዳይ ነው፡፡ በብልህነት ማውጠንጠን፣ አርቆ - ማስተዋል፤ ነገሮች ተደራርበው ግራ እንዳይጋቡን ይጠቅመናል፡፡ የሙስና ላይ ዘቻው አንድ ረድፍ ነው፡፡ የቤት ችግር ሠልፍ፣ ለቤት የተመዘገበ ሰው ያገኘው ኮንዶምኒየም በሌላ ተወስዶበት ለአቤቱታ ቤት - ደጁን ማጥለቅለቅ፤ እናቱ የሞተችበትም፤ ወንዝ የወረደችበትም እኩል ማልቀሳቸው፤ መንግሥት ላይ ዕምነት ማሳደር ባንድ ወገን፣ መንግሥት በትክክል ሊቆጣጠረው ባይችልምስ የሚል ፊናንሳዊ ስጋት በሌላ ወገን፤ አፍንጫችን ሥር ያሉ ጉዳዮች ናቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ በጦርነት ድንፋታ ንፋስ ከታጀቡ ደግ አይሆንም፡፡

ስለጦርነት ከተነገሩት ድንቅ አነጋገሮች ሁሉ የሚከተለው ይገኝበታል - “ጦርነት ነፃነትህን ስለሚወስድብህ አስፈላጊ የሆነ ምርጫ ላይ ለመዋጋት ወይም ላለመዋጋት ልትወስን ትችላለህ፡፡ አንዴ ጦርነት ከገባህ ግን የምርጫ ኃይልህ አከተመ” (ጊልበርት ሙሬይ) ሁሉም ነገር ጥንቃቄንና ዝግጁነትን ይጠይቃል፡፡ የተረጋጋ ህዝብን ይጠይቃል፡፡ መንገዶች ሁሉ ወደአንድ አቅጣጫ እንዳይሄዱ፤ እመነገጃውና እመገበያያው የሚገቡትን ባለይዞታዎች በጥሞና መያዝ ይገባል፡፡ የህዝብን አመኔታ የሚያጠናክር አዎንታዊ እርምጃ ሀገራዊ ስሜትን ለማድመቅ እጅግ ወሳኝ ነው፡፡ ቤትም አገርም አለኝ የሚል ህዝብ እንዲኖረን ያስፈልጋል! “በሰው ልጅ ላይ የወረደ ታላቅ መርገምት ጦርነት ነው፡፡

በሰላም ጊዜ የሚፈፀሙት የጭካኔ ወንጀሎች፤ በሰላም ጊዜ የሚካሄዱት ሚስጥራዊ ሙስናዎች አሊያም የሀገሮች ሃሳብ - የለሽ የገንዘብ ዝርክርክነቶች ሁሉ፤ ጦርነት ከሚያደርስብን ሠይጣናዊ ጥፋት ጋር ሲወዳደሩ እንክልካይ ነገሮች ይሆናሉ” ይለናል፤ ሲድኒ ስሚዝ፡፡ የህዝብን የልብ ትርታ ማዳመጥ የወቅቱ ጥሪ ነው፡፡ የመንግሥት ጥንቃቄ የተሞላ እርምጃም የወቅቱ ጥሪ ነው፡፡ ዲሞክራሲያዊና ዲፕሎማሲያዊ ሂደትን ሥራዬ ብሎ ማቀናጀት ብልህነት ነው!! ዕውነት ገና ጫማውን እያሰረ፣ ውሸት ዓለምን ዞሮ ይጨርሳል የሚለውን አባባል አንርሳ!! በመላና በጥበብ የመምራት ክህሎትን የሚጠይቅ ወቅት ነው፡፡ “አዞው ወደውሃ ሲስብ፣ ጉማሬው ወደ ሣሩ ይስባል” የሚለው የወላይታ ተረት ጉዳያችንን ያሳስበናል፡፡

Published in ርዕሰ አንቀፅ

ይህች ጽሑፍ በአንድ ወቅት በአንድ የመንግስት መስሪያ ቤት አብሮኝ ይሰራ ስለነበር ናሆም የተባለ ወንደ ላጤና ስለሰራተኛው ገበያነሽ (ጋቢ) የምንጨዋወትባት አሪፍ ወግ ናት፤ ዘና በሉ… ቅድመ - ወግ ናሆም እድሜው በሃያዎቹ አጋማሽ የሚገኝ ምርጥ ልጅ ነው፤ በቃ ሙድ የገባው፣ የአራዳ ልጅ የምትሉት አይነት … ተቆራርጣ የምትደርሰው የወር ደሞዙ ባለ አራት ዲጂት ልትሆን ትንሽ የቀራት … በዛችው ደሞዙ ቤት ተከራይቶ ተመላላሽ ሰራተኛ ቀጥሮ የሚኖር … “እቺን ደሞዝ በምን አይነት ብልሃት ነው የምታብቃቃት?” ሲባል “በአስማት” የሚል፣ ኑሮን ቀለል አድርጎ የሚኖር ምርጥ ልጅ … ገበያነሽ፣ እንደ ናሆም ሁሉ ሙድ የገባት ስትሆን፣ ጎበዝ፣ የ10ኛ ክፍል የማታ ተማሪ ናት፡፡ ናሆም ጨምሮ ወደ አምስት የሚደርሱ ወንደ-ላጤዎች ጋር በመስራት ራሷን የምታስተዳድር ሁለገብ ፍሪ-ላንሰርም ነች … ጋቢ በጠዋት ተነስታ የሁለት ወንደ-ላጤ ቤቶችን ስራ አቀለጣጥፋ ጨርሳ፣ ናሆም ቤት ወደ አራት ሰዓት ገደማ ትደርሳለች፡፡

ናሆም ደግሞ ከእሁድ በስተቀር ከሁለት ሰዓት በፊት ከቤቱ ስለሚወጣ ከጋቢ ጋር የሚገናኙት በ “ሜሞ” (አጭር የፅሁፍ ማስታወሻ) ነው፡፡ የናሆምና የጋቢ ሜሞዎች ትዕዛዝና መረጃ ከመለዋወጫነት በዘለለ ስለ ብዙ ጉዳዮች በስፋት የሚያወጉበት፣ የሚቀላለዱበት፣ የሚበሻሸቁበት፣ የሚደናነቁበት … ወዘተ ነው፡፡ እነዚህ ብጫቂ ወረቀቶች በሁለቱ መካከል ያለውን ንፁህ እህታዊና ወንድማዊ ግንኙነት ቁልጭ አድርገው የሚያሳዩ ሲሆኑ፤ ስነፅሁፋዊ ይዘታቸዉም የሚናቅ አይደለም፡፡ ሜሞዎቹን ሲያሻቸው በእንግሊዝኛ፣ አልያም በአራዳ ቋንቋ ስለሚፅፏቸው አንዳንድ ጊዜ ከፅሁፍ ይልቅ ወሬ ቢመስሉም ስርዓተ-ነጥብን ሳይቀር በአግባቡ ያካተቱና አንዱ ከሌላው በቅርፅም በይዘትም የማይገናኙ ናቸው፡፡ አስቂኝ ወሬ ወይም ተረባ በመሃከል ካለ የሳቅ ድምፃቸውን ሁሉ ሳያስቀሩ ያስገባሉ፤ ናሆም - ካካካካ … ጋቢ - ቂቂቂቂ … እያለች፡፡ ደስ ብሏቸው ይፃፃፋሉ … አንዱ የሌላውን ለማንበብ ይቸኩላል … እንኳን እነሱ እኛም ሳንቀር የቢሮ ስራችንን የምንጀምረው በእኒህ አዝናኛ ፅሁፎች ነበር፡፡

እንደውም፣ እነዚህን ፅሁፎች ማሳተም አለብህ እያልኩ እወተውተው ነበር፡፡ ወደፊት “የወንደ-ላጤናውና የሰራተኛዋ ሜሞ” በሚል ርዕስ እንደሚያሳትማቸው ከልብ እየተመኘሁ ከሜሞዎቹ በጥቂቱ እነሆ … ፅሁፎቹ እንደወረዱ የቀረቡ ናቸው፡፡ ቀን፡ 10/4/2001 ዓ.ም ይድረስ፡- ለገበያነሽ (Arrive: for Marketing) ካካካካ … ጋቢዬ፣ ዛሬ ጓደኛዬን እቤት ምሳ ስለጋበዝኩት ቤቷን ሰንደል ጨስ አድርጊባትና አሪፍ ምሳ አዘጋጂልን፣ አራት ድንችና ሶስት ራስ ሽንኩርት አለ፡፡ በሱ አሪፍ፣ ጣት የሚያስቆረጥም ጥብስ ፍርፍር ስሪልን … ካካካካ … ለማንኛውም ለእንጀራና ሌላ መግዛት የምትፈልጊው ነገር ካለ ብዬ ኮመዲኖው ላይ ሃያ አምስት ብር አስቀምጬልሻለሁ፡፡ መልስ ካለ እዛው አስቀምጪልኝ፣ በተረፈ መልካም ፈተና፡፡ ናሆም፣ ከማይነበብ ፊርማ ጋር ቀን፡ 10/4/2001 ዓ.ም ይድረስ፡ ለናሆም … ኡኡቴ! አንተን ብሎ ምሳ ጋባዥ … ቂቂቂቂ … ለማንኛውም አራቱ ድንቾች ትንንሽ ስለሆኑ ግማሽ ኪሎ ድንች ገዝቻለሁ፤ ከዛ ውጪ ቲማቲም፣ ሽንኩርትና እንጀራ ገዝቼ የተረፈውን 1 ብር ከ50 ኮመዲኖው ላይ ላስቀምጠው ብዬ እናቴ “ለታላቅ አይመለስም” ትል የነበረው ትዝ ሲለኝ ይዤው ሄጃለሁ … ቂቂቂቂ … በተረፈ በአራት ድንችና በሶስት ሽንኩርት የሚሰራ ጥብስ ፍርፍር ስለማልችልበት አልጫ ድንች፣ ወጥና … ጥብስ … አምሮህ እንዳይቀር ብዬ … ጥብስ ቅጠል ያለው ፍርፍር ሰርቼልሃለሁ … ቂቂቂቂ … ያው ወጡ ከቀዘቀዘባችሁ አሙቃችሁ ብሉ … ዘይት ስለጨረስኩ ለነገ ብር አስቀምጥልኝ፡፡

ቻው፣ ገበያነሽ ቀን 11/4/2001 ዓ.ም ይድረስ ለጋቢያንስ ኧረ ጋቢያችን! ጨዋታ ጨምረሽ የለ እንዴ? የትላንቱ ተረብሽን አልቻልኩትም፣ ልቤ እስኪፈርስ ነው ያሳቅሽኝ … ወጡም በጣም አሪፍ ነበር፣ እኔ እምልሽ፣ ቅቤ ደግሞ ከየት አምጥተሽ ነው? ከሼባው ወንደላጤ ቤት ቋ አድርገሽ እንዳይሆን? ቤተሰብ አደረግሽን እኮ … ካካካካ … በነገራችን ላይ፣ ቤት ውስጥ ምንም አስቤዛ በሌለበት ምግብ የምትፈጥሪው ነገር ብዙም አይገባኝም፣ ለነገሩ እንዲገባኝ አልፈልግም፣ በአስማትም ይሁን በፀሎት ዋናው ቁም ነገር የሚበላ ነገር መኖሩ ነው፡፡ የትም ፍጪው … (Where crash bring my ash) አይደል የሚባለው … ካካካካ … መቼም ባንቺ መላ ባይሆን ኖሮ ይቺ ደሞዜ ሁለት ሳምንት እንኳን በቅጡ እንደማታዘልቀኝ ታውቂዋለሽ፡፡ ለማንኛውም በድጋሚ አመሰግናለሁ፣ የኔ አስማተኛ … ካካካካ … የዘይት ብር ኮመዲኖው ላይ አስቀምጬልሻለሁ፡፡ ፒስ ባይ - ናሆም ቀን 11/4/2001 ዓ.ም ለ፡ እርሶ አንተ ነገረኛ! እንደው ምን ይሻልሃል … ለማንኛውም ወጡ ቅቤ አለው ምናምን ያልከውን ወሬ ቅቤ ያለው እስኪመስል ይጣፍጣል ለማለት ከሆነ ከአንገቴ ሰበር፣ ከወገቤ ጎንበስ ብዬ ተቀብዬዋለሁ … ይህቺ የፈጠርካት ታሪክ ግን ብዙም አልተመቸችኝም፤ እኔኮ ፕሮፌሽናል ነኝ! እንዴት ከአንዱ ቤት ወስጄ ለሌላው እሰራለሁ፣ ከአስራ ሁለት የስነ ምግባር መርሆች መካከል አንዱ ታማኝነት እንደሆነ ረሳኸው? ቂቂቂቂ … ለማንኛውም ሀሳብህን በመርህ ደረጃ ተቀብዬዋለሁ፡፡

ባይሆን ሚስጥሩን ልንገርህ፣ አንዳንድ ጊዜ ምንም አስቤዛ ሳይኖር ምግብ የምሰራልህ ከራሴ ቤት እያመጣሁ ነው፤ ምክንያቱም ስለምታሳዝነኝና ስለምታዝናናኝ … በዛ ላይ ልክ እንደ ወንድሜ ስለማይህ ነው፡፡ በል አሪፍ ምስር ወጥ ሰርቼልሃለሁ፤ አሙቀህ ብላ … ያጠብኳቸውን ልብሶች አልጋው ላይ አጣጥፌ አስቀምጬልሃለው … ብር ስላልነበረኝ እንጀራ አልገዛውልህም፡፡ እደር፣ ጋቢ ይህች ቀጣይዋን ሜሞ ኖሆም በጋቢ የምግብ ዘይት አጠቃቀም በጣም ቅር በመሰኘቱ የፃፋት ናት፡፡ ለአንድ ወር የሚገዛትን አንድ ሊትር ከግማሽ ዘይት እሷ በሁለት ሳምንት ጭጭ ስለምታደርጋት እንዲህ ሲል ፅፎላታል … ለተከበሩ … ጋቢሽካ፣ የትላንቱ ምስር ወጥ በጣም አሪፍ ነበር፤ ነገር ግን ቅባት በጣም ስለበዛበት ነው መሰለኝ ጨጓራዬ ሲነድ ነው የዋለው፡፡ ሌላ ነገር ይሆናል እንዳልል ውጪ አልመገብም፣ ባለፈው ሳምንትም የሰራሽልኝን ድንች ወጥ ቅባቱን እየፈራሁ በልቼው በቃ ምን አለፋሽ፣ አንቆራረጠጠኝ … ስቃጠል ነው የዋልኩት … ለማንኛውም ካሁን በኋላ የምትሰሪልኝ ወጦች ላይ ዘይት በጣም አትጠቀሚ፡፡

በዛ ላይ ደግሞ የልብ በሽታ እንዳለብኝ ነግሬሻለሁ አይደል? በዘር ነው መሰለኝ እኛ ቤት ሁሉም የልብ በሽታ ታማሚ ስለሆነ ለዘይት የሚደረገው ጥንቃቄ ለየት ያለ ነው፡፡ ሰሞኑን ደረጃ ስወጣ ሁሉ ልቤ ድው ድው እያለች ነው፡፡ እናም … ባጭሩ … እንዳልጭርብሽ ለማለት ያህል ነው! ካካካካ … በነገራችን ላይ ሶስቱን የፊዚክስ ጥያቄዎች በትክክል ሰርተሻቸዋል፤ የሆነ የተሳሳትሽው ስቴፕ ነበረ፤ እሱን ምልክት አድርጌበታለሁ፡፡ በደንብ እይው፡፡ ቻው! ናሆም ለ፡ እርሶነቶ … ናሆሜ ለምንድን ነው እስከ ዛሬ ድረስ ያልነገርከኝ! እኔ እኮ ላንተ ማሰቤ ነበር፤ ጣፍጦህ እንድትበላ ብዬ ነው ቅባት የማበዛው፡፡

ለማንኛውም ከአሁን በኋላ አስተካክላለሁ፡፡ አይዞህ! አትጭርም … ቂቂቂቂ … ለልብ በሽታህ ደግሞ ጠዋት ጠዋት ትንሽ ዱብ ዱብ በልባት … ሰሞኑን ብር ሳታስቀምጥልኝ እየወጣህ ስለሆነ ምንም ነገር አልገዛሁልህም፤ ሽሮም የመጨረሻዋን ዱቄት አራግፌ ነው የሰራሁልህ … ለነገ ምን እንደምሰራልህ አሳውቀኝ … ደህና እደር፣ ጋቢ ጋቢ ከተጫዋችነቷና ከምስኪንነቷ ባሻገር የዋህ ቢጤ ናት፤ የነገሯትን ሁሉ አምና የምትቀበል … ከቅርበታቸው የተነሳ ስለ ዘይቱ የፃፈውን ሜሞ አንብባ “በግልፅ ዘይቴን አትጨርሺ አትልም…” ብላ ኩም የምታደርገው መስሎት ነበር፤ ነገር ግን ልጅቷ ጋቢ ናት … አምና ተቀብላዋለች፡፡

በነገራችን ላይ ምንም እንኳን በመሃከላቸው ጥሩ ቅርርብና ግልፅነት ቢኖርም የዘይት ቅነሳውን እውነተኛ ምክንያት ለምን እንዳልነገራት ናሆምን ስጠይቀው እንዲህ ነበር ያለኝ … “ባክህ! እሷ ምስኪን ስለሆነች እንደዛ ካልኳት፣ ዘይት ከራሷ ቤት እያመጣች ልትሰራልኝ ትችላለች፤ ያን ደግሞ እኔ አልፈለግሁም …” የናሆምና የጋቢ መተሳሰብና መዋደድ በጣም የሚያስቀና፣ የሚያዝናና … ብዙ ብዙ የሚባልለት ነው … እስኪ በመጨረሻ ጋቢ ከላይ ለፃፈችው ሜሞ፣ ናሆም የፃፈላትን መልስ አስነብቤያችሁ ወጌን ላብቃ … ለ፡ ጋቢሻ … ጋቢቾ! ፒስ ነው አይደል? ጠፋህ ነው ያልሽው? አንቺ ምን አለብሽ … አምስት ደሞዝ እየበላሽ … ካካካካ … ለማንኛውም የጠፋሁት … ያው እንደምታውቂው አራተኛው ሳምንት አይደል፤ እናም ብር ኔፕ ሆኜ ነው … ለአስቤዣ መግዣ የሚሆን ገንዘብ ስለሌለኝ ለእራት የሆነች ነገር ይዤ እገባለሁ፡፡ ባይሆን “ምን ሰርቼ ልሂድ?” ላልሽው፣ ምንም ሳትሰሪ ከምትመለሺ ፑሻፕ ሰርተሽ ሂጂ … የቻልሽውን ያህል … ካካካካ … ሰራሁልሽ … ካካካካ … ናሆም፣ ቻው!

Published in ህብረተሰብ

ቤት ለማግኘት ትዳር እየፈረሰ ነው (ግን ፌክ ነው!)

 አንዲት የሥራ ባልደረባዬ እህት አለች - ነገር የምታውቅ፡፡ (ነገረኛ አልወጣኝም!) ጨዋታ አዋቂ፣ ተረበኛ፣ ቀልድና ፌዝ መፍጠር የሚሆንላት ማለቴ ነው። ፈረንጆቹ humorist እንደሚሉት፡፡ እናላችሁ… በሳምንት አንድ “የሰቀለ” ቀልድ ወይም ተረብ አታጣም - እቺ የባልደረባዬ እህት፡፡ አንዳንዱ ደሙን የሚያመርትበትን ጉዳይ እሷ ቀልዳ ትዝናናበታለች፡፡ ለራሷ መዝናናት ብቻ ሳይሆን ለሰውም ትተርፋለች። የሳቅና የጨዋታ ምንጭ ናት - በአጭሩ፡፡ ይሄንን ችሎታ ለማን እንደተመኘሁት ታውቃላችሁ? ለአገሬ ፖለቲከኞች - ለገዢውም ለተቃዋሚውም፤ ለወጣቱም ለአዛውንቱም፤ ለገጠሩም ለከተሜውም፤ ለአገር ቤቱም ለዳያስፖራውም፤ ለምሁሩም ለተማሪውም በቃ ሁሉም ቀልድ አዋቂና ተጫዋች ቢሆን እንዴት ይመቸኝ ነበር መሰላችሁ! እኔማ እነኢህአዴግ ብቻ ሳይሆኑ ራሱ መንግስትም (ኢህአዴግና መንግስት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው እንዳትሉኝ!) ቀልድ አዋቂና ተጫዋች ቢሆን ደስታውን አልችለውም! (ለራሱም ደስታ እኮ ነው) ዲስኩር አበዛሁ አይደል… አሁን ወደቁም ነገሩ፡፡

ያቺ የባልደረባዬ እህት ሰሞኑን ምን አለች መሰላችሁ? “የኢህአዴግ ሰልፍ ከእሁዱ የሰማያዊ ፓርቲ ሰልፍ በለጠ እኮ!” ግራ ገባኝ፡፡ ኢህአዴግ መቼ ነው ሰልፍ የጠራው - ለራሴ ያቀረብኩት ጥያቄ ነበር፡፡ ሌላው ቢቀር በኢቴቪ አይዘገብም እንዴ? እንኳን የ”ገዢያችን” ሰልፍ የሰማያዊ ፓርቲ ሰልፍ ተዘግቧል እኮ (አንዳንዶች “ተንኮል ታስቦ ነው” ቢሉም) ነገርየው እንዳልገባኝ ተናገርኩ - ኢህአዴግ ስላደረገው ሰልፍ አላውቅም በማለት (ከ2002 ምርጫ በኋላ ማለቴ ነው!) ለካስ እሷ የምትለው ሌላ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሂሳብ ደብተር ለመክፈት የተሰለፈውን ህዝብ ማለቷ ነው - ቤት ፈላጊውን፡፡

በእርግጥ ይሄኛውም ሰላማዊ ሰልፍ ነው “የመኖሪያ ቤት ብሶት የወለደው የአዲስ አበባ ነዋሪ” ቤት ለማግኘት ያደረገው ሰልፍ!! ሁለቱም ሰልፎች እኮ አንድ ናቸው - የኢህአዴግም የሰማያዊ ፓርቲም፡፡ እንዴት አትሉም? ሁለቱም የመብት ጥያቄ ላይ ያተኮሩ ናቸው፡፡ ልዩነታቸው ምን መሰላችሁ? አንዱ በተቃውሞ፣ ሌላው በድጋፍ መደረጋቸው ነው፡፡ (የባንኩን እንደ ድጋፍ ሰልፍ ቁጠሩት) ግን እኮ የአዲስ አበባ ነዋሪ ሰልፍ መውጣት ከጀመረ ከረምረም ብሏል፡፡ ቆይ መቼ ነው ለታክሲ መሰለፍ የተጀመረው? እውነቴን እኮ ነው…የትራንስፖርት ወረፋም እኮ ሰላማዊ ሰልፍ ነው - በውዴታ ሳይሆን በግዳጅ የሚደረግ፡፡ (ዕድሜ ለኢህአዴግ!) እኔ የምለው ግን… በቃ ባቡሩ ሥራ ካልጀመረ የትራንስፖርት ችግር ላይፈታ ነው!፡ ትንሽ ተስፋ ያደረግሁት ምን ነበር መሰላችሁ? ከአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓል ጋር ተያይዞ የታክሲ ወረፋ እልባት ያገኛል ብዬ ገምቼ ነበር፡፡

(ለእንግዶቹ ሲባል የማንሆነው የለም ብዬ እኮ ነው!) ሆኖም ግምቴ ግምት ሆኖ ቀረ፡፡ ሰሞኑን ደግሞ ምን ወሬ እንደሰማሁ ታውቃላችሁ? ከአዲስ የመኖሪያ ቤት ፈላጊዎች ምዝገባ ጋር በተገናኘ ውልና ማስረጃ ቢሮ በፍቺ ማመልከቻ ተጨናንቋል አሉ (የጋብቻ ፍቺ እኮ ነው!) ወይ ጉድ! ቤቱ ሲገኝ ጋብቻው ፈረሰ ማለት እኮ ነው! ፍቺው ግን የምር አይደለም አሉ፡፡ “ፌክ” ፍቺ ነው! ፍቺውን የሚፈጽሙት ቤት ለማግኘት ነው፡፡ ባልም ሚስትም በነፍስ ወከፍ አንድ አንድ ኮንዶሚኒየም እጃቸው ለማስገባት ህጋዊ ትዳራቸውን ይቀዳሉ (ጊዜው ከፍቷል!) ግን እኮ ህጋዊ ያልሆነ ትዳር ይቀጥላል! በዲቪ አሜሪካ ለመሄድ ስንቱ “ፌክ” ጋብቻ እየፈፀመ የተሳካለትም ጉድ የሆነም እንዳለ እናውቃለን፡፡ አሁን ደግሞ “ፌክ” ፍቺ መጣ እየተባለ ነው፡፡ በነገራችሁ ላይ መስተዳድሩ በአዲሱ የቤት ፈላጊዎች ምዝገባ “ህገወጦችን ለጠቆመ 15 በመቶ ወሮታ ይከፈለዋል” ብሏል፡፡ ህገወጦችን ጠቁሞ ገንዘብ ማግኘት እኮ ክፋት የለውም፡፡ እኔን ያሳሰበኝ ምን መሰላችሁ … ነገርየው እንደ ዋና መተዳደርያ እንዳይቆጠር ነው! (የፖሊስ ስራ መስሎኝ!) እኔ የምላችሁ … የህዳሴው ግድብ ጉድ አፈላ አይደለ! (እዚህ ሳይሆን ካይሮ!) እውነት ግን ምንድነው ግብፆቹ የሚሉት? (በ21ኛው ክ/ዘመን ጦርነት ማሰብ እኮ “ሼም” ነው!) ከሁሉም ደግሞ ምን ገረመኝ መሰላችሁ?

ለአደባባይ መብቃት የሌለበት ውይይት (ውይይት ሳይሆን ሴራ እኮ ነው!) በስህተት በቲቪ ላይቭ ተላለፈ መባሉ ነው! ቅድም የጠቀስኩላችሁ የባልደረባዬ እህት፤ የግብፅ ተቃዋሚዎች በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት ለመክፈት መመካከራቸውን ስትሰማ፤ እንደ አብዛኞቻችን “ዘራፍ” ለማለት አልቃጣትም። የግድቡ ጉዳይ እንደሚመለከታት የገለፀችው “ከህዳሴው ጋር እኮ ቦንድ አለኝ!” በማለት ነው። (ቅኔ እኮ ነው!) እንግዲህ ሰሙ የገዛቸውን ቦንድ የሚጠቁም ነው፡፡ (ባለ 50 ሺ ወይም ባለ 100ሺ ከዚያም በላይ ሊሆን ይችላል) ወርቁ ደግሞ Bond ከሚለው የእንግሊዝኛው ቃል ይመዘዛል - ትስስር፣ ቁርኝት፣ እትብት፣ ደም፣ እናት አገር… እንደ ማለት ነው፡፡ አንዱ ወዳጄ ደግሞ “የዋህ ናቸው” አለ - የኢትዮጵያ መንግስት ላይ የሸፈቱ አማፂያንን ለመደገፍ በምስጢር ተመካክረዋል የተባሉትን የግብፅ ተቃዋሚዎች፡፡ “እነዚህ ምን የዋህ ናቸው … አደጋ እንጂ!” አልኩኝ - ድንገት ወኔዬ ተነስቶብኝ፡፡

“የኢትዮጵያን ታሪክ ባያውቁ ነው!” “እንዴት ማለት … እነሱ እኮ ሃሳባቸው አማፂያንን እያስታጠቁ ኢትዮጵያን ሰላም ሊነሱ ነው!” “የሚታጠቅላቸው ሲያገኙ አይደል …” “ቆይ ምን እያልክ ነው … አማፂያን እንደግፋችሁ ሲባሉ እምቢ ይላሉ ነው የምትለው?” ጠየቅሁት፤ ግራ ገብቶኝ “ዓላማቸው የህዳሴው ግድብ እንዳይሰራ መሆኑን እያወቀ ከእነሱ ጋር የሚያብር ኢትዮጵያዊ የለም!” አለኝ ፍርጥም ብሎ፡፡ “መንግስት በትጥቅ ትግል እንጂ በሰላም እሺ አይልም ብለው የሸፈቱትስ?” በጥርጣሬ የተጠቀለለ ጥያቄ ሰነዘርኩኝ፡፡ “በመንግስት ላይ የሸፈተ እኮ በአገሩ ላይ ሸፈተ ማለት አይደለም … ኢትዮጵያዊ በአገሩ ጉዳይ ቀልድ አያቅም … አንድ ነው!” አለኝ በእልህ ተሞልቶ፡፡ (እንደ አፍህ ያድርገው አልኩት - በልቤ!) እስቲ ከአባይ ጉዳይ ወጥተን ደግሞ ወደ ሰላማዊ ሰልፍ እንግባ (እንሰለፍ አልወጣኝም!) ቅድም የጠቀስኩት፣ የሰማያዊ ፓርቲ የተቃውሞ ሰልፍ ጉዳይ ማለቴ ነው፡፡

ጠዋት ላይ የተካሄደውን የተቃውሞ ሰልፍ ኢህአዴግ ማታ በኢቴቪ ተቃወመው አይደል! (ተቃውሞን በተቃውሞ ማለት እኮ ነው!) ይሄውላችሁ … ኢህአዴግ ለምን ሰልፉን ተቃወመ እያልኩ አይደለም (ህገመንግስታዊ መብቱ ነው!) እኔ ማንሳት የፈለግሁት ሰማያዊ ፓርት ጉዳያቸው በፍ/ቤት የተያዘ ተከሳሾችን “ይፈቱ” ሲል መጠየቁ በህግ ስርዓቱ ላይ ጫና ለማድረስ ድብቅ የፖለቲካ ዓላማ እንዳለው የሚያሳይ ነው በማለት “ህገ መንግስት ጥሷል” … ሲል መወንጀሉን በተመለከተ ነው፡፡ እንግዲህ የተከሰሱና በፍርድ ሂደት ላይ ያሉ ሰዎችን ጉዳይ ማንሳት (በበጐም በክፉም!) ህገ መንግስት መጣስ ነው ከተባለ … ግለሰቦቹ እንደተያዙ ኢቴቪ ያስተላለፈው ዶክመንታሪ ፊልም ጉዳይም እንዳይረሳ ለማለት ያህል ነው፡፡ (ጉዳያቸው በፍ/ቤት ውሳኔ ሳያገኝ እኮ ነው ያሰራጨው!) እኔ ግን ለጦቢያ ምን እንደምመኝ ታውቃላችሁ? ህገ መንግስት መጣስና አለመጣሱን ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ (እቅጯን) የሚናገር ዘመናዊ መሳሪያ ማሰራት! እንዴ … ከብዙ ውዝግብ እኮ ነው የሚያወጣን!! አያችሁ… መሳሪያው ከተሰራ ተጠርጣሪውን ይዞ ደሙን ወይም ሽንቱን መመርመር ብቻ እኮ ነው ወይም ሌላ የምርመራ ዘዴ ሊሆን ይችላል፡፡ ከዛ በኋላ ማን ህገ መንግስቱን አክብሮ ይንቀሳቀሳል፣ ማንስ ይጥሳል የሚለውን በደንብ እንለያለን! (መሆንና መምሰል እኮ ይለያያል!) እናላችሁ … የዓለም የፖለቲካ ሳይንቲስቶች ሌላ ዲስኩራቸውን ትተው ይሄን መሳሪያ ቢፈለስፉ ትልቅ ባለውለታችን ይሆኑ ነበር፡፡ ለእኛ ብቻ ሳይሆን ለመላው አፍሪካ!

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ፓርላማ ውስጥ የመነቃቃት ስሜት መፈጠሩን የሚናገሩ አስተያየት ሰጪዎች፤ የምክር ቤቱ አባላት በተለየ ሁኔታ መንቀሳቀስ እንደ ጀመሩ ይገልፃሉ፡፡ በፊት አንድ የሚኒስቴር መ/ቤት ያቀረበውን ሪፖርት አዳምጠው “የሚበረታታ ነው”፣ “መልካም ጅምር ነው” የመሳሰሉ አስተያየቶች ሰጥተው ይሸኙ ነበር ይላሉ - ታዛቢዎች፡፡ አሁን ግን በቀረበው ሪፖርት ላይ ተመስርተው መሞገት፣ የሰላ ሂስ መሰንዘርና ድክመቶችን መንቀስ ጀምረዋል፡፡

“ፓርላማው ጥርስ እያወጣ ነው” ይላሉ፡፡ በዚህ የሚስማሙም የማይስማሙም የም/ቤት አባላት አሉ፡፡

“ፓርላማው ድሮም አሁንም ጥርስ የለውም” - አቶ ግርማ ሠይፉ -

በፓርላማ የመድረክ ተወካይ “ፓርላማው በቅርቡ ጥርስ ማውጣት ጀምሯል በሚለው አልስማማም” -ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ - “የፓርላማውን እንቅስቃሴ የማወዳድረው ከልጅ እንዳልካቸው ዘመን ጋር ነው” - ዶ/ር ዳኛቸው አሠፋ - በአ.አ.ዩ የፍልስፍና መምህር “የፓርላማ አባላት አሁን እየሠሩ ያሉት ቀደም ሲል የሚሰሩትን ነው” - አቶ ታደሠ መሠሉ - የፓርላማ አባል በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመድረክ ፓርቲ ተወካይ አቶ ግርማ ሠይፉ፤ ፓርላማው ጥርስ አውጥቷል በሚባለው ነገር እንደማይስማሙ ይናገራሉ፡፡

“ባይሆን ነቃ ነቃ ብሏል” ቢባል ይሻላል የሚሉት አቶ ግርማ፤ ፓርላማው ድሮም አሁንም ጥርስ እንደሌለውና ለማብቀልም ብዙ እንደሚቀረው ገልፀዋል፡፡ የፓርላማው መነቃቃት ከቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ህልፈት ጋር የተያያዙ ሊሆን እንደሚችል የገለፁት አቶ ግርማ፤ በፊት ጠ/ሚኒስትሩ ሁሉ ነገር ስለነበሩ የፓርላማው ሚና አነስተኛ ነበር ይላሉ፡፡ “አዲሱ ጠ/ሚኒስትር አቶ ኃ/ማሪያም ደሣለኝ ግን አውቀውም ይሁን ሳይውቁ ፓርላማውን በእጅ አዙር የመቆጣጠር አዝማሚያ የላቸውም” የሚሉት አቶ ግርማ፤ የምክር ቤት አባላትም ይህን ዕድል በመጠቀም የሚፈልጓቸውን አካላት ለመቆጣጠር እየሞከሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ምንም እንኳን የፖሊሲ ለውጥ ባይኖርም ሹፌሩ ሲለወጥ በተወሠነ መልኩ ለውጥ እንደሚመጣ ጠቅሠው፤ የጠቅላይ ሚኒስትር ለውጥ የፓርላማውን መነቃቃት እንዲፈጠር ያምናሉ፡፡

ፓርላማው ጥርስ አወጣ የሚባለው መቼ ነው በሚል ተጠይቀው ሲመልሱም፤ “ጥርስ ማውጣት ማለት በስራ አፈፃፀሞች፣ የሚታዩ ጥፋቶችን ሞግቶ አስተማማኝ ድምፅ በመስጠት ሚኒስትሮችን ማስቀየር ሲችል ነው” ብለዋል አቶ ግርማ፡፡ ፓርላማው ይሄ ስልጣን ቢኖረውም ለበርካታ ጊዜያት እንዳልተጠቀመበት በመግለጽ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ጠንከር ያሉ ውይይቶችን ማድረግ እንደጀመረ ተናግረዋል፡፡ “ሁሉም ሚኒስትሮች ሲመጡ ከፓርላማ ተወካዮች የሚቀርቡት ጥያቄዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጠነከሩ መጥተዋል” ያሉት አቶ ግርማ፤ ቀደም ሲል “አበረታች ነው”፣ “ገንቢ ነው” በማለት የሚታወቁ የፓርላማ ተወካዮች፤ “ልክ አይደላችሁም”፣ “በደንብ አልሰራችሁም” ማለት መጀመራቸው ትልቅ ለውጥ መሆኑን አልሸሸጉም፡፡ ሆኖም “ጥርስ አውጥቷል” እስከሚለው አያደርስም ብለዋል፡፡ አቶ ግርማ አንድ ስጋት አላቸው፡፡ “የፓርላማ አባላቱ ዘንድ መነቃቃቱ የተፈጠረው ከጠ/ሚኒስትር ለውጥ ጋር ተያይዞ ነው የሚል አዝማሚያ ከታየባቸው ጠርናፊዎች ወደ ቀድሞ ዝምታቸው ሊመልሷቸው ይችላሉ” ብለዋል፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፍልስፍና መምህር የሆኑት ዶ/ር ዳኛቸው አሠፋ በበኩላቸው፤ “የአሁኑን የፓርላማ እንቅስቃሴ የማወዳድረው ከልጅ እንዳልካቸው ዘመን ጋር ነው” ይላሉ፡፡ “ከተሞክሮዎች እንደሚታወቀው አንድ ጠንካራ ሠው ከቦታው በሚነሳ ጊዜ የፖለቲካ ክፍተት ይፈጠራል” ያሉት ዶ/ር ዳኛቸው፤ በዚህ ጊዜ የተለያዩ አካላት እንደሚበረቱ ገልፀው፤ የሀገራችን ፓርላማም እዛ ሠዓትና ወቅት ላይ እንዳለና ይህ ከፍተኛ እንቅስቃሴ የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን ሞት ተከትሎ እንደመጣ ግምታቸውን አስቀምጠዋል፡፡ የፓርላማ እንቅስቃሴው ቀጣይነት ቢኖረው ጠቀሜታው የጐላ እንደሆነ የገለፁት ምሁሩ፤ “የእኔ ስጋት የተወሠነ ቡድን ወይም ሀይል ጫና አሣድሮ ይሄ ጭላንጭል እንዳይጠፋ ነው” ብለዋል፡፡ “የፓርላማው ስራ ሁለት ነው፤ አንዱ ህግ ማውጣት ሲሆን ሌላው የተለያዩ መስሪያ ቤቶችን እየተከታተሉ የስራ አፈፃፀማቸውን መገምገም ነው” የሚሉት ዶ/ር ዳኛቸው፤ አሁን እየታየ ያለው የፓርላማ አባላት እንቅስቃሴና ጠንካራ ሙግቶች በጣም አስገራሚ በመሆኑ ጅምሩን ልናበረታታ ይገባል ብለዋል፡፡

“እኔ በሁኔታው በጣም እየተረገምኩ ነው፤ ይህን ሁሉ ጉልበት ከየት አመጡት? እስከዛሬ የት አስቀምጠውት ነበር?” ሲሉ የጠየቁት ምሁሩ፤ ይህንን ጠንካራ እንቅስቅሴ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ሞት ጋር የሚያያይዙት “አቶ መለስ አትናገሩ ብለዋቸዋል” ለማለት ሳይሆን ብዙ የሚያውቅ ሠው ባለበት ቦታ የሌሎች አንገት መድፋት በፖለቲካ ውስጥ የሚከሠትና የተለመደ በመሆኑ ነው ይላሉ፡፡ “የፓርላማ አባላት ሁሉንም ነገር ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ያውቃሉ” ብለው ሥለሚያምኑ ለመናገር ድፍረት ያንሳቸው እንደነበር እገምታለሁ” ሲሉም አስረድተዋል፡፡ በተለይ አሁን ከፍተኛ ሙግትና ትችት እያነሱና በድፍረት እየታገሉ ላሉት ሴት የፓርላማ ተወካዮች ትልቅ አክብሮት እንዳላቸው የገለፁት ዶ/ሩ፤ በተለይም “ይህን ጉዳይ ሌላ ስም አጥቼለት ነው፤ ግን ሌብነት ነው” ሲሉ በሙስና በተጠረጠሩ ሙሠኞች ላይ ትችት ለሠነዘሩት ሴት የፓርላማ ተወካይ ያላቸውን አድናቆት ገልፀዋል፡፡ ስለፓርላማው እንቅስቃሴ ከወዲሁ ድምዳሜ ከመስጠት ግን ተቆጥበዋል፡፡ የፓርላማውን እንቅስቃሴና ቀጣይነት ወደፊት የምናየው ይሆናል በማለት፡፡

የኢህአዴግን ፖሊሲ እደገፋለሁ የሚሉት በፓርላማ የግል ተመራጭ የሆኑት ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ፤ የፓርላማውን እንቅስቃሴ በተመለከተ የተለየ አስተያየት አላቸው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ፓርላማው ጥርስ ማውጣት ጀምሯል በሚለው ጉዳይ አልስማማም ባይ ናቸው። ፓርላማው በፊትም መስራት ያለበትን ሥራ እየሰራ መሆኑንና አዲስ የተፈጠረ ነገር እንደሌለም ይናገራሉ። “እኔ ገና በግሌ ተወዳድሬ ፓርላማ ስገባ. አብዛኛው ወንበር የኢህአዴግ በመሆኑ ስጋት ገብቶኝ ነበር” ያሉት ዶ/ር አሸብር፤ የመጀመሪያው ስጋታቸው በአንድ ፓርቲ አብላጫ መቀመጫ የተያዘ በመሆኑ ከፍተኛ ሙግቶችና የሀሳብ መንሸራሸሮች አይኖሩም የሚል እንደነበረ ተናግረዋል፡፡ ሌላው ስጋታቸው ደግሞ በግላቸው ተወዳድረው እንደመግባታቸው በፓርላማው ብቸኛና ባይተዋር እሆናለሁ የሚል እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ “ወደ ፓርላማ ስገባ የጠበቅሁትና ከገባሁ በኋላ ያገኘሁት ሁኔታ ግን በጣም ይለያያል” ያሉት ዶ/ር አሸብር፤ ፓርላማው ሥራ ከጀመረ በኋላ አዋጆች ከመፅደቃቸው በፊት ብዙ ክርክሮች ይደረጉ እንደነበር ተናግረዋል። በብዙዎቹ ሪፖርቶች ላይም ከፍተኛ ክርክሮች፤ ውይይቶችና አስተያየቶች ሲደረጉ መቆየታቸውን በመግለጽ፤ ሰሞኑን የተለየ እንቅስቃሴ እንዳለ አድርጐ መናገሩ ትክክል አይደለም ብለዋል፡፡

በፓርላማው ወደ 16 ያህል ቋሚ ኮሚቴዎች እንዳሉ የጠቆሙት ዶክተሩ፤ እያንዳንዱ ቋሚ ኮሚቴ በተመደበባቸው መስሪያ ቤቶች ቁጥጥር፣ ግምገማና የመስክ ጉብኝት ሳይቀር በማድረግ ሃላፊቱን ሲወጣ መቆየቱንና አሁንም እየተወጣ መሆኑን አስረድተዋል። “በመሆኑም ፓርላማው በሙሉ ቁመናው እየሰራ ነው” ባይ ናቸው፡፡ሰዎች ጉዳዩን እንደ አዲስ የቆጠሩት ለምን እንደሆነ ሲያስረዱም፤ በፓርላማውና በሚዲያው በኩል ያለው ክፍተት እየጠበበ በመምጣቱና ሚዲያዎች የፓርላማውን እንቅስቃሴ በትክክል እየዘገቡ በመሆናቸው ነው ያሉት የፓርላማ ተወካዩ፤ ከበፊትም ጀምሮ እያንዳንዱ መስሪያ ቤት ወደ ፓርላማ ሲመጣ ተጨብጭቦለት ሳይሆን የሚሄደው በደንብ ተጠይቆ፤ ተገምግሞና ተፈትሾ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የፓርላማ አባላት የመገዳደር አቅማቸው የጠነከረው የስራ ልምድ እየጨመረ ሲሄድ ከሚዳብር እውቀት እንጂ ምንም አዲስ ነገር አልተፈጠረም” ያሉት ዶ/ር አሸብር፤ “እኔ እንደሚገባኝ በፊት ፓርላማውና ሚዲያው የተገናኙ አልነበሩም፤ አሁን ሚዲያው የፓርላማውን ሙግትና ፍጭት አጉልቶታል” ሲሉ አስረድተዋል፡፡

በቀድሞው ጠ/ሚኒስትር አለመኖር የተነሳ የፓርላማ ተወካዮች ከፍርሀት ተላቀው መናገር ጀምረዋል በሚለው ጉዳይ ፈፅሞ እንደማይስማሙ የገለፁት ዶ/ሩ፤ “እውነት ለመናገር ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን ጠንቅቄ አውቃቸዋለሁ፤ ሠዎች ሲናገሩ ሲከራከሩና ሀሣባቸውን ሲገልፁ የሚወዱ እንጂ ተፅዕኖ የሚያሳድሩ አልነበሩም” ብለዋል፡፡ ምናልባት እንዲህ አይነት ፍርሀት የሚፈጠረው ከአቅምና ከእውቀት ችግር ይሆናል፤ በእውቀቱና በአቅሙ ሙሉ የሆነ ሠው ፍርሃት አያድርበትም ሲሉ አብራርተዋል። “እሳቸው እያሉ እንዴት እናገራለሁ -በጭንቅላትም፣ በልምድም በትምህርትም ይበልጡኛል ብሎ ቅድሚያ ተሸንፎ የገባ አባል ካለ፤ እሱን አላውቅም፤ ነገር ግን በሀሣብና በእውቀት ሙሉ ሆኖ ለቀረበና ለሚገዳደራቸው ሠው ተደስተው ተገቢውን ምላሽ ይሠጣሉ” ብለዋል ዶ/ር አሸብር፡፡ ፓርላማው በአሁኑ ሠዓት አገርን ማዕከል ያደረገ፣ የህዝብን ብሄራዊ ጥቅም የሚያስጠብቅ ክርክር እንጂ የተቃዋሚና የደጋፊ ፓርቲ የሚል አጀንዳ እንደሌለው የገለፁት ዶ/ሩ፤ አላማው ይህቺን አገርና ህዝቧን ከፍ ወዳለ ደረጃ ማድረስ በመሆኑ ድሮ ጥርስ የሌለው አንበሳ ነው፤ አሁን ጥርስ እያወጣ ነው የሚለውን ትተን፣ በአገሪቱ እና በህዝቧ ጥቅም ላይ ፓርላማው አትኩሮ መስራቱን እንዲቀጥል ትኩረት ቢደረግ የተሻለ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ በፓርላማ የኢህአዴግ ተወካይ አቶ ታደሠ መሠሉም፤ ከዶ/ር አሸብር ሃሳብ ጋር ይስማማሉ፡፡

አሁን በፓርላማው እየተሰራ ያለው ድሮም የነበረ እንጂ አዲስ ነገር የለም ይላሉ፡፡ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ሌሎች አስፈፃሚ አካላትን የመከታተል፣ የመቆጣጠርና የመደገፍ ሀላፊነት ተሰጥቶታል ያሉት አቶ ታደሰ፤ እየሰራ ያለውም ይሄንኑ ነው ብለዋል፡፡ ምክር ቤቱ የጐደሉ የስራ አስፈፃሚ በጀቶችንና በአግባቡ ያልተከናወኑ ስራዎችን በተመለከተ መሞገቱ ከዚህ ቀደምም የሚያደርገው እንጂ አዲስ አይደለም ሲሉም አክለዋል፡፡ የፓርላማ አባላት በፊት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስለሚፈሩ አይናገሩም ነበር፤ አሁን በድፍረት መናገር ጀመሩ በሚባለው ጉዳይ ፈጽሞ እንደማይስማሙ የገለፁት አቶ ታደሠ፤ “ለሰው የተለየ ነገር የመሠለው ይህቺን አገር ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ ሲታትሩ ያለፉትን የቀድሞውን ጠ/ሚኒስትር ራዕይ ለማሳካት የፓርላማው አባላት በእልህና በቁጭት መነሳሳታችን ነው” በማለት ብለዋል፡፡ ም/ቤቱ፤ ስራ አስፈፃሚውን ብቻ ሳይሆን የአስፈፃሚውን መሪ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጭምር ጠርቶ የማነጋገር ስልጣን አለው ያሉት የፓርላማ አባሉ፤ ጠ/ሚኒስትሩ ምክር ቤቱ እየጠራቸው ሪፖርትም ማብራሪያም ይሠጡ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ አቶ ታደሰ እንደሚሉት፤ የም/ቤት አባላቱ በየጊዜው በሚያገኙት ሥልጠና ልምዳቸውን እያካበቱ መምጣታቸው፣ ከባለራዕዩ መሪ ሞት ጋር ተዳምሮ በእልህና በወኔ እንዲንቀሳቀሱ አድርጓቸዋል፡፡ ይሄ ማለት ግን ድሮ አይንቀሣቀሱም፤ አይሠሩም ማለት እንዳልሆነ በመጥቀስ የፓርላማው እንቅስቃሴ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ሞት ጋር የሚያገናኘው አንዳች ነገር የለም ብለዋል፡፡

  • “የጦርነት መንገድ ለኢትዮጵያም ለግብፅም አይጠቅምም” - አቶ ሙሼ ሰሙ
  • “ከገዢው ፓርቲ ያነሰ የአገር ፍቅር ያለን አይመስለኝም” - ዶ/ር መረራ ጉዲና

ኢትዮጵያ የአባይን ወንዝ አቅጣጫ መቀየሯንና የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በግብጽና በሱዳን ላይ ሊያደርስ የሚችለውን ተጽእኖ እንዲያጠና የተቋቋመው የኤክስፐርቶች ቡድን ያወጣውን ሪፖርት ተከትሎ፤ የግብጽ ተቃዋሚዎች የህዳሴውን ግድብ ግንባታ ለማስተጓጐል ያቀረቡትን ሃሳብ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች ተቃወሙት፡፡ የግብፁ ፕሬዚዳንት መሐመድ ሙርሲ ከአገሪቱ ባለስልጣናት፣ ከተቃዋሚዎችና ከሃይማኖት ፓርቲዎች ጋር ባደረጉት ስብሰባ፤ በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት ማወጅና፣ የአገሪቱን ተቃዋሚዎች በመደገፍ ኢትዮጵያ የግድቡን ግንባታ እንድታስተጓጉል ማስገደድ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

በስብሰባው ላይ የተንፀባረቀውን ሃሳብ በተመለከተ አስተያየት የሰጡት ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ “በርግጥም ግብፃውያን ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ቀዳዳ አይጠቀሙም ብሎ መከራከር ያስቸግራል፡፡ የአገራችን ተቃዋሚ ፓርቲዎች ግን ለውጭ ሃይል መጠቀሚያ ለመሆን ይዘጋጃሉ የሚል ግምት የለኝም” ብለዋል፡፡ “በአገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች ቢያንስ ቢያንስ ከኢህአዴግ ያነሰ የአገር ስሜት አላቸው ብዬ አልገምትም” ያሉት ዶ/ር መረራ “ይሄም ሆኖ ግን ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት ፈርጀ ብዙ ችግሮች ካልተፈቱ የውጭ ሃይሎች ባገኙት ክፍተት ተቅመው የራሳቸውን ጥቅም ለማስከበር አይሞክሩም ማለት አይቻልም” ብለዋል፡፡ “ከሰባት ዓመት በፊት በፓርላማ የሶማሌን ጉዳይ በሚመለከት ስንወያይ ዳር ድንበራችንን አገራችን ውስጥ ሆነን መከላከል ይሻላል፣ የሰው አገር መግባት አስቸጋሪ ነው፣ እና አሜሪካ እንኳን ያን ያህል ሃብትና ቴክኖሎጂ ይዘው በድል መውጣት አልቻሉም” ብለን ለቀድሞው ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ ሃሳብ አቅርበን ነበር፡፡ እሳቸው ግን “በእኔ ይሁንባችሁ ጥቂት ሳምንት ብቻ ነው በዚያ የምንቆየው” ሲሉን ነበር፡፡

ኢትዮጵያ አሁንም እዚያው ነች፤ ያ ቀዳዳ አለ፤ የኦጋዴን፣ የኤርትራ፣ የሱዳን ቀዳዳዎች አሉ፡፡ የውጪ ሃይሎች እነዚህን ክፍተቶች ለመጠቀም አይሞከሩም ማለት አይቻልም፡፡ የአባይ ወንዝን በሚመለከት ከገዥው ፓርቲ ያነሰ የአገር ፍቅር አለን የሚል ግምት የለኝም ብለዋል ዶ/ር መረራ፡፡ አቶ ሙሼ ሰሙ በበኩላቸው፤ “የግብፅ መንግስት በአገር ውስጥ ያሉና በሰላማዊ ትግል የሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚዎችን የፈለጋቸው፣ የራሱን አጀንዳ ለመሸጥ እንጂ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የመልካም አስተዳደር የፍትህ እጦት አሳስቦት አይደለም፣ የአባይ ግድብ እንዳይገደብ ተቃዋሚዎችን መሳሪያ አደርጋለሁ ብሎ መነሳቱ አግባብ አይመስለኝም፣ ለኢትዮጵያ የሚጠቅም አጀንዳ ስላልሆነ ትርጉም የለውም” ብለዋል፡፡

“መሐመድ ሙርሲ፤ የኢትዮጵያ መንግስትንና ህዝቡን አከብራለሁ የሚል አስተያየት ሲሰጡ በቅርብ ሰዎቻቸው ተሰምተዋል፡፡ በደጋፊዎቻቸውም ይሁን በህዝቡ ወይም በማንም ተባባሪ ሃይል ቢታገዝም፣ የጦርነት መንገዱ ብዙ ርቀት አያስኬድም፡፡ የጋራ ጥቅማችንን ለማስከበር በሩ ክፍት እስከ ሆነ ድረስ ተቀራርቦ መነጋገር እንጂ፣ በጦርነት መልኩ ማሰብ ዘመኑ የሚፈቅደው አይደለም፡፡ በጉዳዩ ላይ ጥናት እንዲያደርጉ በስምምነት ኃላፊነት የተሰጣቸው አካላት ያወጡትን ዝርዝር ሰነድ መመልከትና በምስራቅ አፍሪካ አገሮች የሚገኙ ህዝቦችን መጥቀም የሚችልበትን አቅጣጫ መከተል ነው የሚበጀው፡፡ የጦርነት መንገድ ለኢትዮጵያም ለግብፅም አይጠቅምም” ብለዋል፡፡

Published in ዜና

ሰማያዊ ፓርቲ ዋና ዋና ያላቸውን አራት የህዝብ ጥያቄዎች በመያዝ ባለፈው ግንቦት 25 ያካሄደውን ሰላማዊ የተቃውሞ ሠልፍ፣ የገዢው ፓርቲ ባለስልጣናት እና የመንግስት ተወካዮች “የሀይማኖት አክራሪነት አጀንዳ” ነው ማለታቸው ተልካሻ አስተያየት ነው ሲል ሰማያዊ ፓርቲ ተቃወመ፡፡ “መንግስት ሠማያዊ ፓርቲ ህጋዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሠልፍ ባደረገባቸው የህዝብ ጥያቄዎች ላይ ተልካሻ ምክንያቶችን እያቀረበ ከመፈረጅ ይልቅ በሶስት ወራት ውስጥ የህዝቡ ጥያቄዎች እንዲመለሱ በድጋሚ እንጠይቃለን” ብሏል በመግለጫው፡፡ ፓርቲው በትናንትናው ዕለት ባወጣው መግለጫ፤ ሠማያዊ ፓርቲ ከመንግስትም ሆነ ከገዢው ፓርቲ በሚሰጥ የትኛውም ማስፈራሪያ ከጀመረው ሰላማዊ ትግል ፍፁም ወደ ኋላ እንደማይል ገልፆ፤ መንግስት የህዝቡን ጥያቄ እስኪመልስ ትግሉን የበለጠ አጠናክሮ እንደሚቀጥል በመግለጫው አስፍሯል፡፡

ፓርቲው አክሎም፤ መንግስትና ገዢው ፓርቲ በሰጡት አስተያየት፤ “የሀይማኖት አክራሪነትን አጀንዳው አድርጐ ሲንቀሳቀስ የነበረው ሰማያዊ ፓርቲ፣ ዛሬ በጠራው ሰልፍ ድብቅ አጀንዳው ገሀድ ወጣ” በማለት የሰጡት አስተያየት፤ ፓርቲውን ለማንቋሸሽና ለማራከስ የተደረገ በመሆኑ ተቀባይነት የለውም ሲል አጣጥሏል፡፡ “በህጋዊ መንገድ ተጠይቆና ራሱ መንግስት አምኖበት ይሁንታ የሠጠውን እጅግ ሰላማዊ በሆነ መንገድ የተካሄደ ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ፣ ውጭ አገር የሚገኙ ሀይሎች ተላላኪ አድርጐ ማቅረብ “የአብዬን ወደ እምዬ” አይነት ማላከክ ነው ያለው ሰማያዊ ፓርቲ፤ ህገ-መንግስቱ በሚፈቅደው መልክ ዕውቅና አግኝቶ የሚንቀሳቀሰውን ፓርቲያችንን መንግስት እንዳልተቀበለው ተገንዝበናል ብሏል ፓርቲው፡፡ “መንግስት በፓርቲው ላይ እያደረሠ ያለው አጉል ፍረጃ የገዢው ፓርቲ አባላት ለንግግራቸው ሚዛን እንደሌላቸው ያሳያል” ያለው ሰማያዊ ፓርቲ፤ ከፍርጃ ውጭ ሰማያዊ ፓርቲ ከሽብርተኝነት ጋር የሚያገናኘውን አንዳችም ነገር አልጠቀሱም ሲል ተችቷ፡፡

ፓርቲው ቀደም ሲል በሰጣቸው መግለጫዎች በእስልምና እምነት ተከታዮች ላይ የሚደረገውን ጣልቃ ገብነት መቃወሙን አስታውሶ፣ ይህንኑ ጥያቄ በተቃውሞ ሰልፍ ላይ ወደ አደባባይ ይዞ መውጣቱ ህገ-መንግስታዊ የመብት ጥያቄ መሆኑን ገልጿል፡፡ ከባለስልጣኑ የተሰጠው አስተያየት፣ የእስልምና ሀይማኖት ተከታይ ዜጐች በሰላማዊ መንገድ የተቃውሞ ጥያቄ ማቅረባቸውን ተከትሎ ወደ ሽብርተኝነት ፍረጃ ለመክተት የሚያደርገው ጥረት ፓርቲውን በእጅጉ ማስቆጣቱን በመግለጫው አካትቷል፡፡ የትኛውም ፍረጃና ከመንግስት የሚመጣ ማስፈራሪያ ከሰላማዊ ትግሉ እንደማያግደው የጠቀሰው ሰማያዊ ፓርቲ፤ መንግስት በሙስና፣ በሀይማኖት ጣልቃ ገብነት፣ በኑሮ ውድነትና በዜጐች ማፈናቀል ዙሪያ ከህዝቡ የተነሱ አንገብጋቢ ጥያቄዎችን በሶስት ወራት ውስጥ ምላሽ እንዲሠጥ ጠይቋል፡፡

Published in ዜና

1ሚ. ብር አበድሬአቸዋለሁ የሚል ድርጅት ክስ ሊመሰርት ነው የአዋሣው ቤታቸው ተሸጦ ስም መዛወሩ እያነጋገረ ነው

እጅግ የተከበሩ የአለም ሎሬት አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ንብረት እያወዛገበ ነው፡፡ አርቲስቱ በሕይወት ሳሉ አንድ ሚሊዮን ብር አበድሬአቸዋለሁ የሚል ድርጅት ለክስ ወደ ፍርድ ቤት ማምራቱን ምንጮች ገልፀዋል፡፡ ሎሬት አፈወርቅ በህይወት ሳሉ የስዕል ሥራዎቻቸውን፣ ቪላ አልፋንና ሙሉ ንብረታቸውን ለመንግስት ማውረሳቸውን ተከትሎ፣ መንግስት ንብረቱን ለመረከብ እንቅስቃሴ ጀምሮ እንደነበር ይታወቃል፡፡ የእኚሁን ታላቅ አርቲስት ንብረት ለማጣራትና ለመመዝገብም ከፍርድ ቤት፣ ከታዋቂ ሰዎችና ከሙያ ባልደረቦች የተውጣጣ ኮሚቴ ተቋቁሞ ምዝገባና ቆጠራ ቢጀመርም ፍፃሜ ሣያገኝ ተቋርጧል፡፡ ሎሬት አፈወርቅ ተክሌ በህይወት ሣሉ የአክሲዮን ባለ መብት ለመሆን አንድ ሚሊዮን ብር ወስደዋል በሚል የአርቲስቱን ስዕሎች ይሸጥ በነበረ አንድ የማስታወቂያ ድርጅት ክስ ሊመሰረት መሆኑን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

ጉዳዩ በፍርድ ቤት እልባት እንዲያገኝ ለኮልፌ ምድብ ችሎት ተመርቶ እየታየ መሆኑን የጠቆሙት ምንጮች፤ ለጊዜው የንብረት ምዝገባና ቆጠራው መቋረጡን ገልፀዋል፡፡ በአዋሣ ከተማ የሚገኘውና በሎሬት አፈወርቅ ተክሌ ስም የተመዘገበው ቤት በቀድሞ ባለቤታቸው አማካኝነት መሸጡን የጠቆሙት ምንጮች፤ የቤቱ ስም የተዛወረበት አሠራር ሕጋዊነት አነጋጋሪ እየሆነ መምጣቱን ጠቁመዋል፡፡ በሎሬት አፈወርቅ ተክሌ ስም በለንደንና በስኮትላንድ ባንኮች ያለ ገንዘብ እንዲመለስ ጥረት እየተደረገ ሲሆን በተለያዩ አገራት ያሉ ስዕሎችና ንብረቶችን ለማስመለስም እየተሞከረ ነው ተብሏል፡፡ የአርቲስቱ ንብረት ካለባቸው አገራት መካከልም ንብረቱንና ገንዘባቸውን ለመመለስ ፈቃደኛ የሆኑና በመመለስ ሂደት ላይ የሚገኙ እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡

የሎሬት አፈወርቅ ተክሌ ቪላ አልፋ፤ በኮሚቴዎቹ ሲከፈት በሺዎች የሚቆጠር ፓውንድ በካዝናቸው ውስጥ መገኘቱንና ይህም በንብረት ዝርዝር ላይ ተመዝግቦ መያዙን ምንጮች ገልፀዋል፡፡ በፍርድ ቤት ጉዳይ የተቋረጠው የሎሬት አፈወርቅ ንብረት ቆጠራና ርክክብ መዘግየት በንብረቱ ላይ አደጋ ሊያስከትል እንደሚችል የጠቆሙት ምንጮች፤ እጅግ ውድ ዋጋ ያላቸው ስዕሎቻቸውና የአርቲስቱ የመኖሪያ ቤትና የስዕል ስቱዲዮ የሆነው ቪላ አልፋም የመበላሸት አደጋ አንዣቦበታል ብለዋል፡፡ የሎሬት አፈወርቅ ተክሌ የቀብር ሥፍራ ምንም አይነት የማስታወሻ ሐውልት ሣይሰራበት መቅረቱን የጠቀሱት ምንጮች፤ ከጥቂት ጊዜ በኋላ የቀብራቸው ሥፍራ ሊጠፋ ይችላል የሚል ሥጋት መፈጠሩን ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

መንግስት ለውይይት ካልተዘጋጀ 33ቱ ፓርቲዎች ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ አቅደዋል ዋና ኦዲተርና የስነምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ሰሞኑን ለፓርላማ ያቀረቡትን ሪፖርት መነሻ በማድረግ በነገው ዕለት በመድረክ፣ በመኢአድ፣ በአንድነትና በሰማያዊ ፓርቲ ቢሮዎች የፓርቲዎቹ አመራሮች ውይይት እንደሚያደርጉና መድረክ ለሰኔ 17 ህዝባዊ ስብሰባ እንደሚጠራ ተገለፀ፡፡

የመድረክ ስራ አስፈፃሚ አቶ አስራት ጣሴ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ የፓርቲዎቹ አመራሮች በነገው ውይይት የሚደርሱበትን የጋራ መግባባት በመያዝ፣ መድረክ ለሰኔ 17 ህዝባዊ ስብሰባ ለመጥራትና በአዲስ አበባ ከተማ በመዘዋወር የመኪና ቅስቀሳ ለማድረግ ተዘጋጅቷል፡፡ ሙስና የስርአቱ መገለጫ በሆነበት፣ የህዝብ ሃብት እየባከነና የዲሞክራሲ መብቶች እየተጣሱ ባለበት በአሁኑ ወቅት፣ መንግስት እምቢተኝነቱን ትቶ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር ውይይት እንዲያደርግ ጥሪ እንደሚተላለፍለት ገልፀዋል፡፡ ገዢው ፓርቲ የሚቀርብለትን የውይይት ሃሳብ ተቀብሎ ወደ ውይይት ካልመጣ፣ 33ቱ ፖርቲዎች ሰላማዊ ትግሉን ተጠቅመው አገራዊ ንቅናቄ በማድረግ፣ እንደ ሰማያዊ ፓርቲ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ማቀዳቸውንም አስረድተዋል፡፡

Published in ዜና