Saturday, 15 June 2013 11:12

ቀጠሮ

እንደ ማሰላሰያ

አስታውሳለሁ፤ ድሮም እኔ ነበርኩ፡፡አሁንም እኔ ነኝ፡፡ እንደሌሎቹ “እኔ” ብለው ራሳቸውን የሚጠሩ ድሮም አልነበርኩም፡፡ አሁንም አይደለሁ፤ ስጨርስም አልሆንም፡፡ “እና ታዲያ ምንድነው ችግሩ?” ብዬ እጠይቃለሁ፡፡ ጠያቂው እራሴ፤ መልሱን ሳልመልስ ተመልሼ ዝም እላለሁ፡፡ ከድሮውም ፀሃፊ መሆንን እፈልጋለሁ ስል የሰማኝ ማንም የለም፡፡ ምን መሆን እንደምፈልግ ራሴም ለማወቅ ፈልጌ አላውቅም፡፡ እስር ቤት እንደሆነ ግን አውቃለሁ ህይወት፤ ምን መሆን እንደምትፈልግ ወይንም ምን እንደ ሆንክ ሳታውቅ የእስር ዘመንህን ጨርሰህ የምትለቀቅበት፣ ወደነፃነት መልቀቅ የለም፡፡ ሞትም ፤የተወለደ ሁሉ ደግሞ የሚወለድበት አማራጭ የሌለው እጣፈንታ ነው። የመጣውን መቀበል ነው፡፡ እስር ቤቱን ሰብሮ ነፃ የወጣ የለም፡፡ ፀሀፊነትም ነፃ መውጫ አይደለም። የራስን እጣ ፈንታ በድርሰት አለም ገፀ ባህሪዎች ላይ በክፋት መለማመድ ነው፡፡ ክፋቱ ነው ጥሩነቱ፡፡

ክፋትን በክፋት መመለስ ነው የትንሹ ፈጣሪ…የሰው ስራ፡፡ አንድ ወዳጄን ለማግኘት ቀጠሮ ያዝን። በአንድ የእስር ቤቱ ስፍራ፡፡ ብሔራዊ ትያትር ደጃፍ ተባብለን ተቃጠርን፡፡ በብሔራዊ እስር ቤት ውስጥ ጥበበኞች የሚገናኙበት ሁኔታ ራሱ ትያትር ነው። እስረኞች ስለ እስር ቤቱ ሲገልፁ… በትያትር ቤቱ ገለፃቸውን ያቀርባሉ፡፡ ገለፃቸው ሊገልፀው የማይችለው የእሳቱን ክፍል ግን ከቲያትር ቤቱ ውጭ ይኖሩታል፡፡ ኑሮአቸው ሊገለጽ፣ ሊገሰጽም አይችልም፡፡ ለማ? እንዴት ተደርጐ? የቀጠርኩት ወዳጄ ገጣሚ ነው፤ የሙዚቃ አዋቂ ነው፣ የሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጅ እና አቅራቢ ነው፤ የጥበብ መብት አስጠባቂ ነው…ሁሉንም መሆኑ እስረኛ ከመሆን አያድነውም፡፡ ግን የእሱ አይነቶች፤ በእስረኞች ነገድ መሃል ባይኖሩ ትርጉም አልባው እስር እና እስር ቤቱ የእለት ተእለት ተግባሩን አያከናውንም ነበር፡፡ ሽንት ቤቱን የሚያፀዳው ባልኖረ ነበር፡፡

አይጦቹ ወጥመድ ያስፈልጋቸዋል። ካልሆነ በአይጥ ወጥመድ ውስጥ እስረኛው ይወድቃል፡፡ የሞቱትን ካልቀበሩ የሞቱት እነሱን ይቀብሯቸዋል፡፡ የሞቱትን ለመቅበር የሞተውን በህይወት ካለው የሚለይ ዶክተርም ያስፈልጋል። ሁሉም እስረኛ ሆኖ ተወልዶ የሚሞት ቢሆንም በመሞቻው ሰአት የሚቀብረውን ጓዱን በእስር ህያው አድርጐ ማቆየት ይጠበቅበታል፡፡ የህያውነት ህልም የሚመነጨው ከሞት ውስጥ ነው፡፡ ሞት እና መቀበር መድረሻው ሲሆን… መነሻው ይመረጣል፡፡ ከመነሻው እስከ መድረሻ ያለው ጉዞ ደግሞ ህይወት ተብሎ ይጠራል፡፡ በእስር መቆየት መቻል ከነፃነት የበለጠ ይፈለጋል፡፡ የሚፈለገው የማይፈለገውን እንደ ተቃራኒ ያገባዋል፡፡ ከጋብቻው ውስጥ የእስረኛው ሰው ማንነት ይፈጠራል፡፡ በዚህ መሃል እኔና ወዳጄ አለን፡፡ ቀጠሮም አድርገናል፡፡ ቦታም መርጠናል፡፡ ብዙ ቀጠሮ እና ብዙ ምርጫ አለው የህይወት እስር ቤት ቆይታ።

ሁሉም ቀጠሮ ተደማምሮ የሚያመራው ወደ እማይፈለገው ነው፡፡ ሁሉም ቦታ የመጨረሻው ቀጠሮ ተቀጣሪውን የሚያገናኘው መሬት መቀበሪያውን ሊሆን ይችላል፡፡ ከአንዱ ቀጠሮ በኋላ ሌላ ይከተላል፡፡ ይከታተላል፡፡ የቀጠሮ ብዛት እና ከአንዱ ቀጠሮ በማምለጥ በሌላው መጠመድ እድሜን ይጨምራል፡፡ ይደምራል፡፡ ድምሩ ባዶ ነው። ወደማይፈለገው ነው፡፡ ወደማይፈለገው ለማምራት እስረኛ እየተፈላለገ ይገናኛል፡፡ ይገናኛል፣ ይለያያል። ይወያያል፡፡ ወንዴና ሴቴው በቀጠሮ ይተኛኛል፡፡ ከቀጠሮ ሌላ ቀጠሮ ይረገዛል። የተረገዘው ከሆድ ሲወጣ የእስረኛነት ቀጠሮ ተይዞለት ነው፡፡ ሁሉም ቀጠሮ ወደ ማይፈለገው ነው የሚያመራው፡፡ ነፃነት የማይፈለግ ነገር ነው፡፡ ሞት ለህይወት እረፍት ነው፡፡ ህይወት ለሞት ቀጠሮው ነው። በህይወት ቀጠሮ ሞት እየተረገዘ ጽንሱ ይገፋል። እድሜ እንደ ሆድ ይነፋል፡፡ ከዛ ከህይወት እስሩ ወጥቶ ወደ ጐርጓድ ይደፋል፡፡ እየተነፋ ያለው የህይወት ቅጥረኛ የሚደፋውን መቅበር አለበት፡፡ ሞቱን በውስጡ ይዞ በውጭ ሟቹን ይቀብራል፡፡ ያለቅስለታል፡፡ የሚያለቅሰው ለራሱ ነው፡፡

ከራሱ በላይ ለሆነው የራሱ እጣ ፈንታ ያለቅሳል፡፡ ቢቀብረውም ባይቀብረውም ቀባሪ እና ሟች ሊለወጥ በማይችል ውስን የእጣ ፈንታ ጉርጓድ አንድ ላይ ተቀብረዋል፡፡ ለእስር ቤቱ ካቦ የእስር ቤቱ ህግ አይራራለትም። ለሰንሰለት ጐንጓኙ… ሰንሰለቱ ድር አይሆንለትም። የእስር ቤቱን አስተዳዳሪ እስር ቤቱ አያስተዳድረውም…ነፃ በህይወቱ አይለቀውም፡፡ ፍርዱን አያቀልለትም፡፡ ታዲያ ምንድነው ችግሩ? ስል እጠይቃለሁ፤ ወደ ላይ አያለሁ፡፡ መሬታቸው ላይ ያሉ ክዋክብትም በተበየዱበት ሆነው ወደኔ ያያሉ፡፡ እንደኔው ያዝናሉ፡፡ እነሱም እስረኛ ናቸው፡፡ በቀዝቃዛ ጠፈር ላይ በብርሐን ጥፍር የጨለማን ድንቁርና ያደማሉ። ዘላለማዊ ጨለማ በብርሃን ጥፍር ተቧጥጦ ምን መፍትሔ ሊገኝ?! እስረኛ እስር ቤቱን ለመስበር ያደረገው አመጽ ሁሌ የራሱን አእምሮ ሰብሮ በማምለጥ ነው መፍትሔ ሲያገኝ ያየነው፡፡ ከእስር ነፃ የወጣ እብድ ነው ይላሉ፡፡ እብድ በእስሩ ላይ ያኮረፈ…”በእስሩ” የእላይ የሆነ ምስኪን ነው፡፡ ሁሉም ምስኪን ነው፡፡ ሁሉም ማንም ነው፡፡ ጨክኖ የሚመሰክን ወዮለት…በራሱ ደስታን የፈረደ ነው፡፡ ሌሎችን ማስደሰቻ ይሆናል አመፁ፡፡

የነፃነት ህልሙ ግን ሌሎቹን የሚያስፈራ ለእሱ ግን ስቃዩ ነው፡፡ ታዲያ ምንድነው ችግሩ? ስል እጠይቃለሁ …ምንስ ብሆን ማነው የሚጠይቀኝ? ሁሉንም ነገር ማድረግ አልፈልግም…ሁሉንም ማድረግ ግን እችላለሁ፡፡ ሁሉንም ማድረግ ዋጋ የለውም፡፡ ዋጋ የሌለውን ሁሉ ግን አደርጋለሁ፡፡ ነፃ ስለመሆን እሰብካለሁ፡፡ ስብከቴ፤ ክዋክብቶቹ የጠፈርን በጨለማ መደንቆር በብርሃን መርፌአቸው ጠልፈው አንድ ቀን ሙሉ ብርሃን በሰማይ ላይ እንደሚያነጥፉ በጥቅሻቸው እንደሚሰብኩት ነው፡፡ ከዚህ ወዳጄ ጋር ብርሐኖች ሆነን እንዴት ሰማዩን በብርሃን መቅደድ እንደምንችል ልናወራ ነው ቀጠሮ የያዝነው፡፡ የያዝነው ነገር እኛን አይይዘንም። በሰፊው የምናወራው በቀጭኑ አያግባባንም፡፡ ቀጠሮዎች ጥበቃ ናቸው፡፡ ሞትን የምንጠብቅባቸው ፊርማታዎች፡፡ የምንጠብቀው መጓጓዣ አሳፍሮን እየሄደ እንደሆነ ብናውቅም እምንጠብቀው በመምሰል ወደ ቀጠሮአችን እንሄዳለን፡፡ በብዙ ቀጠሮ አንድ ፌርማታ ላይ ሆነን እንጠብቃለን። የምንጠብቀው የምንፈልገውን እንደሆነ እንወያያለን። የሚሆነው ግን የማንፈልገው ነው።

ቀጠሮን “አልፈልግህም” ብትለው እንኳን እርሱ ይፈልግሃል፡፡ ሳትፈልገው ቆይተህ ትሸሻለህ። እሱ ሲፈልግህ ወደ መቃብርህ ፌርማታ ላይ ይጥልሃል፡፡ በተለያየ መቀመጫ ላይ ሆነን የምናወራው በፌርማታው ላይ ቆመን ነው፡፡ ፌርማታው ድሮውኑ መጓጓዣ ነው፡፡ የመቀመጫ ልዩነት ነው ያለን፡፡ ሁላችንም እስረኞች፡፡ ቀድሞ የታሰረ እና ቆይቶ የሚፈታ፣ ቀድሞ የታሰረ ቀድሞ የሚገታ፣ ቀድሞ የታሰረ እና ቆይቶ የሚፈታን ልጅ ብሎ የወለደ አባት …እራሱ እስረኛ ሆኖ ሌሎችን የሚፈታ ጉልበተኛ…መፈታት ወደ ሞት ነው፡፡ ሞት ነፃነት አይደለም፡፡ ሌላ እጣ ፈንታ ነው፡፡ ሌላ ያለመፍጨርጨር እስር፡፡ “እላይ” ሳይሆን “እስር”፡፡ያለ “ከመስበር ወዲያ ሌላ ህላዌ የለም” አልኩት ወዳጄን፤ የአንዱን እስረኛ ግጥም አስታውሼ፡፡ ቀጠሮአችን አገናኝቶናል፡፡ በህይወት አገናኝቶናል በሞትም አይለያየንም፡፡ የነፋን ህይወት በመቃብር ይደፋናል አንገናኝም አንለያይም፡፡ ህላዌ በሙሉ እስር ከሆነ… ህልውና ለህያው ምኑ ነው? ሁሉም ችግር በሆነበት “ምንድነው ችግሩ?” ብሎ የሚጠይቅ…ቢስቅ ማቆም የማይችል ልጅን፣ በሳቁ የሚደማ የካንሰር በሽተኛን እንደመኮርኮር ይቆጠራል፡፡

Published in ልብ-ወለድ

ቦታው ጉርድ ሾላ አካባቢ በሚገኘው ሳህሊተ ማርያም ቤተክርስቲያን ግቢ ነው፡፡ ዕለቱ ግንቦት 29 ቀን 2005 ዓ.ም ከቀኑ በ10 ሰዓት ላይ፤ ያለ ምንም ግርግርና ሁካታ ቤተክርስቲያኑ ደጅ መጥቶ የቆመው ዲኤክስ የቤት መኪና በውስጡ ሙሽሮችን ይዞ ነበር፡፡ ሙሽሪት ቬሎ ለብሳለች። ባልም በሙሉ ልብስ ደምቋል። በሌላ መኪና የመጡ ሁለት የሴት ሚዜዎች አጀቧቸው። የወንድ ሚዜ የለም፡፡ ሙሽሮቹ ደጀ ሰላሙ ላይ ተንበርክከው ፀሎት ማድረግ ጀመሩ፡፡ ሥነ ስርዓቱን ለታሪክ የሚያስቀሩ አንድ የካሜራና አንድ የቪዲዮ ባለሙያዎች አሉ። ሙሽሮቹ ፀሎታቸውን ሲጨርሱ በመጡበት ፍጥነት ተመልሰው ሄዱ። በሳህሊተ ማርያም ቤተክርስቲያን ግቢ ከ10 ደቂቃ በላይ ያልወሰደው ሥነ ስርዓት ትኩረት ሳቢ ስለነበር ከሙሽራው ስልክ ቁጥር እንድቀበል ገፋፋኝ፡፡ እሱም ፈቃደኛ ሆነልኝ፡፡

በተለያዩ አገራት፣ ሕብረተሰብና ባህሎች በተለያየ መልኩ ተግባራዊ እየሆኑ ለዛሬ ከደረሱ ልማዶች አንዱ ጋብቻ ነው፡፡ ከግራ ጎኑ በተወለደች አጥንት ተሰርታ፤ ሚስቱ ከሆነችው ሔዋንና ከባሏ ከአዳም ጀምሮ የጋብቻ ሥነ ስርዓት ብዙ አስገራሚ ታሪኮችን እያስመዘገበ ለዛሬ ደርሷል፡፡ 33 ዓመት በምድር የቆየው ኢየሱስ ክርስቶስ በተለይ በመጨረሻው ሦስት ዓመታት አስገራሚ ተአምራትን መሥራት የጀመረው በቃና ዘገሊላ በተገኘበት ሠርግ ቤት ውሃውን ወደ ወይን ጠጅነት በመቀየር ነው፡፡ በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ በሠርግ ወቅት የተከሰቱ አስደማሚ ገጠመኞች ተሰብስበው ቢፃፉ (በዚህ ዙሪያ የተሰራ ነገር መኖሩን አላውቅም) ዳጎስ ያሉ በርካታ መፃሕፍት ሊዘጋጁበት የሚችል ነው ነው፡፡ ባለፈው ሳምንት በዚሁ ጋዜጣ ላይ “አዝናኝ ትዝታ” በሚል ርዕስ በመድኃኔ ዘካርያስ የቀረበው የሠርግ ገጠመኞች ለዛሬው ጽሑፍ መነሻ ሆኖኛል፡፡ ለሕብረተሰብ መሠረት የሆነው ጋብቻ ሲፈፀም፤ በየሠርግ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የሚታዩ አስገራሚ፣ አስተማሪ፣ አዝናኝ፣ አናዳጅ … ሁነቶች ይከሰታሉ፡፡

ባለ ሀብቶች፣ ምሁራን፣ መንፈሳዊ ሰዎች … ሲያገቡ በየሠርግ አዳራሹ ብዙ ታሪክ ታይቷል፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት እንኳን አንዳንድ የአገራችን ታዋቂ አትሌቶች በታሪክ ሊጠቀሱ የሚችሉ የሠርግ ሥነ ሥርዓቶችን ፈጽመዋል፡፡ አትሌት ኃይሌ ገብረ ሥላሴ፣ በአትላንታ ኦሎምፒክ አሸንፎ ሲመጣ አየር መንገድ ግቢ ውስጥ የቀለበት ሥነ ሥርዓት በመፈፀም ነበር ባለትዳር የሆነው፡፡ የአትሌት ቀነኒሳ በቀለ ሠርግ ደግሞ በ35 ሚሊዮን ብር በተሰራ የመናፈሻ ቦታ ላይ ነበር የተካሄደው፡፡ በሒልተን ሆቴል መስመር የሚገኘውና አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ፣ አፍሪካ የሚል ሦስት የተለያዩ ክፍሎች ያሉት የመናፈሻ ሥፍራ፤ በሼህ መሐመድ ሁሴን አላሙዲን ልግስና በአዲስ መልክ ከተሰራ በኋላ፣ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው በአትሌት ቀነኒሳ በቀለ የመሞሸሪያ ዕለት እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ አትሌት ገዛኸኝ አበራ፣ ሠርጉን በአዲስ አበባ ስታዲየም በማሰናዳት ብቻ ሳይሆን ባለቤቱ የምትለብሰው ቬሎ 600 ሜትር ርዝመት እንዲኖረው በማድረግ በዓለም ሪከርድ ለመመዝገብ ሞክሯል፡፡ በጊነስ ቡክ መመዝገብን ዓላማ ያደረገ የሠርግ ሥነ ስርዓት ደግሞ በቅርቡ በአዲስ አበባ ትንሿ ስታዲየም ተከናውኗል።

በዚህ ሠርግ ላይ ሙሽራውና ሙሽሪት እያንዳንዳቸው 100 ሚዜዎችን፣ በድምሩ 200 ሚዜዎች በማሰለፍ የልዩ ታሪክ ባለቤት ለመሆን በቅተዋል። እነዚህ ጥንዶች እግረ መንገዳቸውን ለሠርጋቸው የጠሯቸው ሰዎች የአመለካከትና የሥራ ፈጠራ ክህሎት እንዲያገኙ ባለሙያዎችን በመጋበዝ እንዲያስተምሩላቸው አድርገዋል፡፡ በተለያዩ ሠርጎች ላይ ጋብቻ ፈፃሚዎች በሚለብሱት ልብስ፣ በሚያዘጋጁት አዳራሽና የምግብ ዓይነት፤ በሚጓዙበት የትራንስፖርት ዓይነት፤ በሚያጅቧቸው መዘምራን፣ ፈረሰኞች፣ ሞተር ባይስክሎች፣ ጋሪዎች … የተለዩ ለመሆን ሲጥሩ ይታያል፡፡ ውድ በሆኑ ሊሞዚንና ሠረገላ ከመሞሸር ባሻገር ለሠርጋቸው ሒሊኮፕተር የሚከራዩ ተጋቢዎች እየታዩ ነው፡፡ ተጋቢዎች ልዩ ታሪክ ለማስመዝገብ ወይም አስተማሪ መልዕክት ለማስተላለፍ የሚጠቀሙበት ዘዴ አንዳንዱ ከፍ ያለ ወጭን ሲጠይቅ፣ከፊሉ የገንዘብ ብክነትን ሲያስቀር ይታያል፡፡

በቅርቡ ሥራና ታሪካቸው በዚሁ ጋዜጣ ላይ የቀረበላቸው ዶክተር ማይክል ዳንኤል አምባቸው (ዐፈሩ ይቅለላቸው) “የትዳር አጋሬን ከወላጆቿ ቤት ወደ እኔ ቤት የማመጣት መኪና ተከራይቼ ሳይሆን በግል ቮልስ ዋገን መኪናዬ ነው” ብለው በተግባር አሳይተዋል፡፡ በሠርጋቸው ዕለት አስተማሪ ተግባራትን ካከናወኑ ኢትዮጵያዊያን መካከል የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህሩ “የኔታ” አለማየሁ ሞገስ ምሳሌነትን መጥቀስ የግድ ይላል፡፡ በ1954 ዓ.ም “ሠርግና ልማድ” በሚል ርዕስ ባሳተሙት መጽሐፋቸው፤ የማይጠቅሙንና ጎጂ ባህሎቻችን ናቸው የሚሏቸውን ለማስወገድ፤ የራሳቸውን የጋብቻ ሥነ ስርዓት ባልተለመደ መልኩ ስለመፈፀማቸው ዝርዝር ታሪኩን በመጽሐፉ አቅርበዋል፡፡ ባልተጠበቁ መንፈሳዊ ጉባኤዎች ላይ፤ በዩኒቨርስቲ የተማሪዎች መመረቂያ መድረክ፤ ለሠርግ ሥነ ስርዓት በማይታሰቡ ዕለትና ሰዓታት … የተለያዩ ጋብቻዎች ሲፈፀሙ ይታያል፡፡ ግንቦት 29 ቀን በሳህሊተ ማርያም ቤተክርስቲያን ግቢ በአጋጣሚ ያገኘኋቸው ሙሽሮችም በዚህ ክፍል ሊመደቡ የሚችሉ ናቸው፡፡ በዕለተ ሐሙስ፣ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ሙሽሮች ብቻቸውን በቤተክርስቲያን ግቢ ይገኛሉ ብሎ ማሰቡም ሆነ መገመቱ ያልተለመደ ይመስላል፡፡ አቶ ብዙአየሁ በላይ የቴሌኮሚኒኬሽን ሠራተኛ ሲሆን ወ/ሮ የዓለምዘውድ ተስፋዬ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህር ናት፡፡

የዛሬ 8 ዓመት የግል ኮሌጅ ተማሪ ሳሉ የጀመረው ትውውቃቸው እያደገ መጥቶ በጋብቻ ተሳስረው አብረው ለመኖር ከወሰኑ አንድ ዓመት አስቆጥረዋል፡፡ ሠርጋቸውን ቀላልና ቀልጣፋ ለማድረግ ብዙ አስበውበታል፡፡ ሙሽሪት ለሚዜነት የመረጠቻቸው ሁለት እህቶቿን ነው፡፡ አቶ ብዙአየሁ ሚዜ አያስፈልገኝም ብሏል፡፡ ለትራንስፖርት መኪና ቢከራዩም በአበባ አሳምረው ትኩረት መሳብ አልፈለጉም፡፡ ቀድመው ወደ ሙሽሪት ቤት ሽማግሌዎች ከመላካቸው ውጭ ሁሉም የሠርግ ሥነ ሥርዓት በአንድ ቀን ነው ያለቀው፡፡ ሐሙስ ጠዋት እሷም ከቤቷ፣ እሱም ከመኖሪያው ወጥቶ ቦሌ ክፍለ ከተማ ጋብቻ ማፈራረሚያ ቢሮ ተገኙ፡፡ በዕለቱ ብዙ ሙሽሮች ስለነበሩ በመቀመጥ ጊዜያችንን ከምንጨርስ ብለው ወደ ፎቶ ስቱዲዮ ሄዱ፡፡

ቀለል ያሉ ፎቶግራፎችን ከተነሱ በኋላ ለምሳ የጠሯቸው 40 እንግዶች ወደሚጠብቋቸው ሬስቶራንት አቀኑ፡፡ ከምሳ በኋላ እንግዶቻቸውን አሰናብተው በክብር መዝገብ ላይ ለመፈራረም ወደ ቦሌ ክፍለ ከተማ ሄዱ፡፡ ያንን ሲጨርሱ በሲኤምሲ አካባቢ ወደሚገኘው የአትሌቶች መንደር መኖሪያ ቤታቸው ሲሄዱ እግረ መንገዳቸውን በሳህሊተ ማርያም ቤተክርስቲያን የፀሎት ሥነ ስርዓት አከናወኑ፡፡ “ብዙ ተጋቢዎች ያልተገባ ወጭ በማውጣት ለጭቅጭቅና ለትዳር መፍረስ ምክንያት የሚሆኑ ተግባራት ሲፈጽሙ ማየታችን የእኛን ሠርግ ቀላል ለማድረግ አነሳስቶናል” ያሉኝ ሙሽሮቹ ፣ “ሕይወት ከአንድ ቀን ደስታና ጭፈራ በላይ ትርጉም ያለው ነገር ነው፡፡ ሕይወት ስለ ነገ ማሰብን ይጠይቃል፡፡ ይህን ሃቅ መረዳታችን ነው ሠርጋችንን ቀላል ያደረገው” ብለዋል፡፡

በአገራችን በየዓመቱ 9ሺ ሴቶች የፌስቱላ ችግር ያጋጥማቸዋል፤ ህክምና የሚያገኙት ግን 1200 ብቻ ናቸው

              “ለባል የተሰጠሁት ገና ከእናቴ ጀርባ ላይ በአንቀልባ እያለሁ ነው፡፡ ዕድሜዬ ከፍ እያለ ሲሄድ ቤተሰቦቼ ትምህርት ቤት አስገቡኝ ለትምህርት ግጥም ሆንኩ፡፡ ጐበዝ ተማሪ ስለነበርኩ መምህራኖቼ በጣም ይወዱኝ ነበር፡፡ 3ኛ ክፍል ላይ ስደርስ ትምህርቴን አቋርጬ ትዳር እንድይዝ በቤተሰቦቼ ተገደድኩ፡፡ አሻፈረኝ ብልም የሚሰማኝ አጣሁ። በደረቁ እየላጩ በእግር ብረት እያሰሩ ትዳር አስያዙኝ፡፡ በዕድሜ እጅግ ከሚበልጠኝ ባለቤቴ ጋር የግብረ ስጋ ግንኙነት ማድረግ የጀመርኩት የአስራ ሁለት ዓመት ልጅ እያለሁ ነው፡፡ ከዛም አረገዝኩ፡፡ ስለ እርግዝና ምንም የማውቀው ነገር ባለመኖሩ ተጨነቅሁ፡፡

ልጁን ከሆዴ አውጥቼ መጣል ተመኘሁ፡፡ ግራሩን በደረቴ አድርጌ ወገቤን አርቄ ይዤ ዝም ብዬ አምጣለሁ፡፡ ልጁ ሊወጣልኝ አልቻለም፡፡ ቀኔ ደርሶ ምጤ ሲጀምረኝ የማውቀው ነገር አልነበረኝም፡፡ ለአራት ቀንና ሌሊት ሳምጥ ቆየሁና ወለድኩ፡፡ ልጁ ከነህይወቱ ቢወጣም እኔ ግን ተበላሸሁ፡፡ አጥንቴ ተፈረከሰ፡፡ የሽንት ቆባዬ ፈነዳ። ሽንቴ ሲወርድ አልሰማውም፡፡ ሰውነቴ በሽንት ሲዘፈቅ ይታወቀኛል እንጂ ሲወርድ አላውቀውም ነበር፡፡ ግራ ቢገባኝ እናቴን ጠየኳት፡፡ እናንተ ከወለዳችሁ በኋላ ሽንታችሁን ስትሸኑ ይታወቃችኋል ወይ አልኳት፡፡ አዎ እኛ ይታወቀናል አለችኝ፡፡ ታዲያ እኔ ምን ሆኜ ነው ስላት ቆሌው ተጣልቶሽ ነው አለችኝ፡፡ ግራ ገባኝ፡፡ ሰገራዬና ሽንቴ ተቀላቅሎ እየወረደ እስከ ፀጉሬ ድረስ ይነክረኛል፡፡

ቤቱና አካባቢው ሁሉ በመጥፎ ሽታ በመታጠኑ ሰው ሁሉ ተጠየፈኝ፡፡ እናቴ ጠፈሩን አልጋ ጀንዲዉን ቀዳ ይንጠፍጠፍ ብላ እዚያ ላይ ሰቀለችኝ፡፡ ሠገራ እንዳይመጣኝ ምግብ አልበላም፡፡ የአጓት ውሃ እየጠጣሁ ህይወቴን አቆየኋት፡፡ እናቴ በሁኔታዬ በጣም ታዝን ነበር፡፡ ድሮውንም እብድ ነበርሽ በቃ ሆጭ ብለሽ አረፍሽው ትለኛለች፡፡ ባለቤቴ በየአዋቂው ቤት ይዞኝ መዞር ጀመረ ግን ምንም መፍትሔ አላገኘሁም፡፡ የወለድኩትን ህፃን ሣየው እነቂው እነቂው ይለኛል፡፡ እንዲህ የተበላሸሁት በሱ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ ቤተሰቦቼም ቆሌው ተጣልቷት ማህፀኗን አፍርሶ ጣለው ይሉኛል እንጂ ምንም መፍትሔ ሊሰጡኝ አልቻሉም፡፡ እንዲህ እያልኩ ለሃያ ስምንት አመታት ኖርኩ፡፡ ከዕድሜዬ ግማሽ የሚበልጠውን ያሣለፍኩት መኝታ ላይ ነው፡፡ እዛው አልጋዬ ላይ ሆኜ ከበኸር ልጄ ሌላ አስራ አንድ ልጆችን ወልጃለሁ። ባለቤቴ ገንዘቤን ሁሉ ባንቺ ጨረስኩ፡፡

እኔም ባንቺ ስንከራተት ደከመኝ ይለኛል። እዛው መኝታዬ ላይ ሆኜ ግንኙነት እንድናደርግ ይጠይቀኛል፡፡ እኔ እንኳንስ እንደዚህ ሆኜ ፊቱንም ፍላጐት የለኝም፡፡ እናም እምቢኝ እለዋለሁ፡፡ ግን ያስገድደኛል፡፡ ሁለት ቀን ባቸንፍ አንድ ቀን እገኛለሁ፡፡ ምን ላድርግ የሰው እህል እየበላሁ ሰው ቤት ተቀምጬ እንቢ ብዬ የት እደርሳለሁ። እያስገደደ ይገናኘኛል፡፡ እንዲህ እያልኩ እዛው መኝታ ላይ ሆኜ በሙት አካሌ አስራ ሁለት ወለድኩ፡፡ ይህን ሁሉ ልጅ ወልጄ እንኳን ፈርምልኝና ላዛውር ብለው ፈቃደኛ አልሆነልኝም። የአካባቢዬ ሰዎች ዝም ብለሽ ስትወልጂበት ይተውሻል ይሉኛል። እርግዝናዬን እንጂ ምጤን አላውቀውም። እያማጥኩም አልወለድኩም፤ በቃ በዛው በተከፈተው ውልቅ እያሉ ይወጣሉ። ይህንን ሁሉ ልጅ በመውለዴ እኔ ብጐዳም በሽታው እየጠናብኝ እየተበላሸሁ ስሄድ መቼም ልጅ ልጅ ነውና ከዝንብ ይከላከሉኛል ይከውኑኛል የሚል ተስፋ አድርጌ ነው፡፡ አገር ምድሩ ተጠይፎኝ ሽንትና ሰገራዬ ዝም ብሎ እየወረደ፣ ለሃያ ስምንት ዓመታት ከኖርኩ በኋላ፣ ለበሽታዬ መድሃኒት አለ መባሉን ሰምቼ ጐንደር መጣሁ፡፡ ወደ ጐንደር ስመጣ ቤተሰቦቼ ፍቃደኞች አልነበሩም፤ የነበረው በሽታሽ ይሻልሻል። አፈራርሰው ነው የሚገድሉሽ እያሉ ያስፈራሩኝ ነበር። ግን ወሰንኩ። በቃ ከሞትኩም ሐኪም አይቶኝ ልሙት አልኩና መጣሁ፡፡ መርፌና ኪኒና ጀመርኩ። ብዙም ሣይቆይ ህመሙ እየታገሰልኝ ሄደ፡፡

የወር አበባዬም ቆመ። በ2003 ዓ.ም ህክምናው ተሠራልኝና ዳንኩ፡፡ ማመን አቃተኝ፡፡ ለካ በሽታው አብሮኝ የተፈጠረ አይደለም። ለካ ይድናል ብዬ በጣም ተገረምኩ። ከሰው ተገልዬ ሰው ሣይቀርበኝ ለሃያ ስምንት አመታት የኖርኩት ሴትዮ፣ ሰው ማግኘት ከሰው መዋል ጀመርኩ፡፡ ተመስገን እንጂ ሌላ ምን ይባላል፡፡” ይህንን አሳዛኝ ታሪካቸውን ያጫወቱኝ በአማራ ክልል በጐንደር ዙሪያ ወረዳ ማክሰኚት ፅዮን ስኳች ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት ወ/ሮ ነገሥ መስፍን ናቸው። የአርባ አራት አመቷ ወ/ሮ፣ በህመምና በሥቃይ የቆዩባቸው ሃያ ስምንት አመታት በቃላት ሊገለፅ በማይችል መጠን እጅግ ከባድ እንደነበሩ ይናገራሉ። በሆስፒታሉ ከአካላዊ ሕክምና በተጨማሪ የሥነ ልቡና ሕክምና ተደርጐላቸው ዛሬ ሙሉ በሙሉ ጤናቸው ተመልሷል፡፡ የእኚህ እናት ታሪክ በአገራችን በአብዛኛው የተለመደና የብዙ ሴቶች ታሪክ የሆነ ጉዳይ ነው። በተለይ በአማራው ክልል አካባቢ የወ/ሮ ነገሥ መስፍን አይነት ታሪክ ያላቸውን ሴቶች ማግኘት ቀላል ነው፡፡ ለዚህ ዋንኛ ምክንያቱ ደግሞ በአካባቢው የሚካሄደው ሴት ልጆችን ያለ ዕድሜ መዳር ያስከተለው ተፅዕኖ ነው፡፡ የጐንደር ዩኒቨርሲቲ ሆስፒታል አለም አቀፍ የፌስቱላ ስልጠና ማዕከል በአለም አቀፍ ደረጃ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚከበረውን የፌስቱላ ቀን ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም “To End obstetric Fistula” በሚል መሪ ቃል አክብሮ ነበር፡፡ እ.ኤ.አ በሐምሌ 2011 ዓ.ም ተመርቆ ሥራውን የጀመረው ማዕከሉ፣ እስከ አሁን ድረስ 550 ለሚደርሱ የፌስቱላ ህሙማን ህክምና ሰጥቷል፡፡

በማዕከሉ ለህክምና ከሚመጡት ህሙማን አብዛኛዎቹ የሚመጡት ከአማራው ክልል ገጠርማ አካባቢዎች ነው፡፡ ከህሙማኑ በርካታዎቹ እድሜያቸው ከ15 ዓመት በታች ሲሆን የሰባት ዓመት የፌስቱላ ተጠቂ ሕፃንም በማዕከሉ በህክምና ላይ እያለች አግኝተናታል፡፡ በማዕከሉ ተኝተው ህክምናቸውን እየተከታተሉ ከሚገኙት ህሙማን ከ98 በመቶ በላይ የሚሆኑት ህመሙ ያጋጠማቸው ያለ ዕድሜያቸው በሚፈፅሙት ወሊድ ምክንያት ሲሆን ችግሩ የመጀመሪያ ልጃቸውን በሚወልዱበት ጊዜ የሚፈጠር ነው፡፡ የአስራ ሶስት አመት ዕድሜ ያላት ታዳጊ ለዓለም፣ ከጠለምት አድርቃይ ወረዳ ጐንደር ሆስፒታል አለም አቀፍ የፌስቱላ ስልጠና ማዕከል የመጣችው በወሊድ ሰበብ የደረሰባትን የፌስቱላ ችግር ለመታከም ነው፡፡ ታዳጊዋ ያለ ዕድሜዋ ተድራ ያለ ጊዜዋ በመውለዷ ሳቢያ የፌስቱላ ችግር ሲያጋጥማት ባሏ ጥሏት ሄዷል። በጐንደር ዙሪያ የደብረ አምባ ዳንጐሬ ወረዳ ነዋሪዋ ፍሩንስ መንጌም የዚህ ችግር ሰለባ የሆነችው በወሊድ ሣቢያ ነው፡፡ ፍሩንስ ለባል የተሰጠችበትን ወይም የታጨችበትን ዘመን አታውቀውም፡፡

በእናቴ ጀርባ ላይ በአንቀልባ ሆኜ ነው የታጨሁት ትላለች። ዕድሜዋ ትንሽ ከፍ ሲል ያጫት ሰው ወደቤቱ አስገባት፡፡ በሁለቱ ተጋቢዎች መካከል ያለው የዕድሜ ልዩነት የአባትና የልጅ ያህል ይራራቃል። ገና ቦርቃ ያልጠገበችው ህፃን፣ ጐጆ ወጣሽ ስትባል ትርጉሙም አልገባት፡፡ ከእናት ከአባቷ ቤት አስወጥቶ ቤቱ ያስገባት ጐልማሣም ባሏ እንደሆነ ጨርሶውንም አታውቅም፡፡ ኧረ እንደውም ባል ማለት ምን እንደሆነ የምታውቀው ነገር አልነበራትም። ጐልማሳው ባል ከቤቱ ያስገባትን ታዳጊ እንደ ልጁ ሣይሆን እንደ ሚስቱ ሊያስተዳድራት ከቤተሰቦቿ ፈቃድ አግኝቷልና ገና ያልጠነከረ ሰውነቷን ተገናኝቶ በአስራ አራት አመቷ አረገዘች፡፡ እርግዝናዋ ከአቅሟ በላይ ነበረና እጅግ ፈተና ሆነባት፡፡ ምንም አይነት የህክምና እርዳታ ለማግኘት በማትችልበት ሁኔታ ለአራት ቀንና ሌሊት አምጣ ህይወት የሌለው ልጅ ወለደች፡፡ በምጥ ያሳለፈችባቸው አራት ቀናት እጅግ ከባድ ከመሆናቸው የተነሣም ፅንሱ በማህፀኗ ላይ ጉዳት አድርሶ የሽንት ፊኛዋንና የሰገራ መውጫዋን አቀላቀላቸው፡፡

በዚህም ሽንትና ሠገራዋን መቆጣጠር ፈፅሞ ተሣናት፡፡ በሽታው ከሰው አራራቃት፡፡ በለጋ ዕድሜዋ ከቤተሰቦቿ እቅፍ ወስዶ ለዚህ ችግር የዳረጋት ባለቤቷም ተጠየፋት፡፡ በሽተኛ ምን ያደርግልኛል፤ እኔ ወደ ጤናማዋ መሄዴ ነው ብሎ ጥሎአት እብስ አለ፡፡ በዚህ የስቃይና የመከራ ጊዜዋ የደረሰባትን መገለልና ችግር ስታወራ እምባና ሣግ ያቋርጣታል፡፡ የወሬ ወሬ የሰማችው ጉዳይ ልቧን አሸፈተውና አዲስ አበባ በመከራ መጣች፡፡ እሷን የመሰሉ ህሙማን የሚታከሙበት ሆስፒታል ከአዲስ አበባ መኖሩን የነገሯት ሰዎች ሥፍራውን በአግባቡ ጠቁመዋት ኖሮ አዲስ አበባ ፌስቱላ ሆስፒታል መጥታ ህክምና ጀመረች፡፡ ከህመሟ ተፈውሣ ወደ አገሯ ስትመለስ ቤተሰቦቿ ማመን ተሳናቸው፡፡ እንደ ልቧ ወዲያ ወዲህ እያለችና እየሰራች ኑሮዋን ትገፋው ጀመር፡፡

የኑሮ ውጣ ውረዱና እንግልቱ እንደ እሷ ላለ ጉዳተኛ ከባድ ነበረና ሕመሙ ድጋሚ አገረሸባት፡፡ ጐንደር ፌስቱላ ማዕከል ገብታ በድጋሚ ህክምናው ተደርጐላት አሁን ከበሽታዋ ድናለች፡፡ የተለያዩ ከባድ ጉልበትን የማይጠይቁ ሥራዎችን እየሰራች ኑሮዋን ትደጉማለች፡፡ ገነት አድማሱ፣ ታልፊያለሽ ማሙዬና አዛቡ ዋጋው እንደ እነ ወ/ሮ ነገሥ መስፍንና እንደ ፍርኑስ መንጌ ሁሉ በወሊድ ምክንያት የፌስቱላ ችግር ያጋጠማቸውና በማዕከሉ ህክምናቸውን በመከታተል ላይ የሚገኙ ህሙማን ናቸው፡፡ በ13 ዓመት ዕድሜዋ ተደፍራ በማርገዟ ሣቢያ ቤተሰቦቿ ከቤት አባረዋት ያለ ማንም እገዛና ድጋፍ ለብቻዋ በጫካ ውስጥ ከአምስት አሰቃቂ የምጥ ቀናት በኋላ ህይወት የሌለው ልጅ ተገላግላ የፌስቱላ ችግር ያጋጠማት ሴት ተመሳሳይ ታሪክም የፌስቱላ ችግር አሰቃቂው እውነታ ነው፡፡ በ60 ዓመት ዕድሜያቸው ለፌስቱላ ችግር የተጋለጡት የሞጣ ወረዳም ወ/ሮ የተመኝ መርሻም የፌስቱላ ችግር ዕድሜን የማይለይና በማንኛውም የዕድሜ ክልል ላይ ሊከሰት የሚችል ችግር መሆኑን አመላካች ናቸው፡፡ ለኪንታሮት ህመም መድሃኒት ነው በሚል የባህል አዋቂ ነኝ ካለ ግለሰብ በሲሪንጅ የተወጉትና ምንነቱን የማያውቁት ነገር ወ/ሮ የተመኝን ለፌስቱላ ችግር ዳርጐአቸዋል፡፡

ዕድሜና ችግር ያደከመው ሰውነታቸው፣ በሽታውን ለመቋቋም አቅም ነስቷቸዋል፡፡ በማዕከሉ ህክምና ለማግኘት ከመጡ ሰነባብተዋል፡፡ ማዕከሉ እንደዚህ ላሉ ከተለያዩ አካባቢዎች ለመጡ የፌስቱላ ተጠቂዎች ከሚሰጠው ህክምና በተጨማሪ የምርምርና የስልጠና ማዕከል በመሆንም ያገለግላል፡፡ ፌስቱላ ሁለት በተፈጥሮአቸው ውስጣቸው ክፍት የሆኑ የሰውነታችን ክፍሎችን የሚለያየው አካል በጉዳት ሲበሣና ሁለቱን ክፍተቶች ሲያቀላቅል የሚከሰት የጤና ችግር ነው፡፡ በሽንት ፊኛና በሰገራ መውጫ አካባቢ በተለያዩ ምክንያቶች በሚደርስ ጉዳት ሣቢያ ሁለቱን የሰውነት ክፍሎች የሚለያየው ስስ አካል ሲበሣ ወይም ሲቀደድ የፌስቱላ ችግር ተፈጠረ ይባላል፡፡ በዚህ ምክንያት ጉዳቱ የደረሰባት ሴት ሽንቷንም ሆነ ሠገራዋን ለመቆጣጠር ሣትችል ትቀርና ለከፋ የአካልና የሥነ ልቡና ጉዳት ትዳረጋለች፡፡ ችግሩ በወቅቱ ህክምና ካላገኘ ጉዳት የደረሰበት የሰውነት ክፍል ኢንፌክሽን ይፈጥርና ህመምተኛዋ መዳን ለማይችል ጉዳት ወይንም ለሞት ልትዳረግ ትችላለች፡፡ የፌስቱላ ችግር በአብዛኛው የሚከሰተው በሴቶች ላይ ሲሆን እጅግ ጥቂት የሚባሉ ወንዶች በሠገራ መውጫቸው ላይ በሚደርስ ጉዳት ሣቢያ ለፌስቱላ ችግር የሚዳረጉበት አጋጣሚ አለ፡፡

የማህፀንና የፅንስ ስፔሻሊስቷ ዶ/ር አምባዬ ወ/ሚካኤል እንደሚናገሩት፤ ፌስቱላ በተለያዩ ምክንያቶች ሊፈጠር የሚችል ቢሆንም በአገራችን በብዛት የሚታየውና የብዙ ሴቶች ችግር የሆነው በወሊድ ምክንያት የሚከሰተው የፌስቱላ አይነት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ያለ ዕድሜ የግብረ ስጋ ግንኙነት በማድረግ፣ በቀዶ ህክምና ወቅት በፊኛ ላይ ጉዳት ሲደርስና በተፈጥሮ ማህፀን ዝግ ሲሆን የፌስቱላ ችግር ሊፈጠር ይችላል፡፡ ከወሊድ ጋር በተያያዘ ምክንያት የሚከሰተው የፌስቱላ ችግር “ዩሮ ጄኔታል ፌስቱላ” በአብዛኛው ዕድሜያቸው ለወሊድ ብቁ ባልሆኑ ሴቶችና ማህፀናቸው ጠባባ በሆኑ ሴቶች ላይ የሚከሰት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በምጥ ወቅት የፅንሱ አቀማመጥና አመጣጥ የተዛባ ከሆነና ልጁ ትልቅ ሲሆን በእናቲቱ ማህፀን ላይ የመተርተር ችግር ከመፍጠሩም በላይ በፊንጢጣ ላይ ጉዳት በማድረስ ለፌስቱላ ችግር ያጋልጣል፡፡ የአንዲት ሴት ምጥ በሃያ አራት ሰዓት ውስጥ መጠናቀቅ ይኖርበታል፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ እናቲቱ ፅንሱን መገላገል ካልቻለች ልጁ ማህፀኗን ይጫነዋል፡፡

ይህም በፊኛዋና በሠገራ መውጫዋ ላይ ጫና በመፍጠር በቀላሉ እንዲጐዳና የደም ዝውውሩ እንዲቋረጥ ያደርገዋል፡፡ በዚህ ወቅት ተጐጂዋ እርዳታ ካላገኘች በሽንት ፊኛዋና በፊንጢጣዋ አካባቢ ያሉት ህዋሳቶቿ ይበሰብሱና ቀዳዳ ይፈጥራሉ፡፡ በዚህ ጊዜም ተጐጂዋ ሽንቷንም ሆነ ሠገራዋን መቆጣጠር ይሣናታል፡፡ ችግሩ መጥፎ ጠረንን የሚፈጥር በመሆኑ ታማሚዋ ከሰው ትገለላለች፡፡ ይህ ደግሞ በሥነ ልቦና ላይ ችግር በመፍጠር ተጐጂዋን ለከፋ ጉዳት እንደሚያጋልጣት ዶክተር አምባዬ ይናገራሉ፡፡ የጐንደር ዩኒቨርሲቲ የህክምና ትምህርት ቤት ኃላፊ፣ የአለም አቀፍ ፌስቱላ ማሰልጠኛ ማዕከል የፕሮጀክት አስተባባሪና የማህፀንና የፅንስ ስፔሻሊስት የሆኑት ዶ/ር ሙላት አደፍርስ እንደሚገልፁት፤ በማዕከሉ በሙያው በሰለጠኑ ሐኪሞች በሚደረገው ህክምና 90 በመቶ የሚሆኑት የችግሩ ተጠቂዎች ከበሽታቸዉ ይድናሉ፡፡ ህክምናው ለችግሩ መፍትሔ ለማስገኘት ያስችላል፤ ሆኖም በግብረ ሥጋ ግንኙነት ወቅት የህመም ስሜት መኖር፣ የወር አበባ አለማየትና፣ መውለድ አለመቻል ህሙማኑን ሊያጋጥሙ የሚችሉ ችግሮች ናቸው፡፡ ወደ ማዕከሉ ለህክምና የሚመጡ አብዛኛዎቹ ሴቶች በቤተሰቦቻቸው የተገለሉ በመሆናቸው ህክምናቸውን ሲያጠናቅቁ ወደ ነበሩበት ቦታ እንዲመለሱ ማድረጉ እጅግ አስቸጋሪ ነው፡፡ ስለዚህም እነዚህ ሴቶች ራሳቸውን የሚችሉበትን መንገድ ማመቻቸትና ራስን ማስቻል ማዕከሉ እያከናወናቸው ካሉ ተግባራት ውስጥ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

ማዕከሉ የተቋቋመው የፌስቱላ ችግር በስፋት በሚታይበት በአማራው ክልል አካባቢ መሆኑ የችግሩ ተጠቂ የሆኑ ሴቶች ህክምናውን በአፋጣኝ ለማግኘት እንዲችሉ ዶ/ር ሙላት ይናገራሉ፡፡ በጐንደር ዙሪያ በሚገኙ ወረዳዎች ውስጥ ያሉት ጤና ጣቢያዎች የችግሩ ተጠቂ የሆኑ ሴቶችን ወደ ማዕከሉ በመላክ የህክም እርዳታ ለማግኘት እንዲችሉ እንደሚያደርጉም በዚሁ ጊዜ ተገልጿል፡፡ ከእነዚህ ጤና ጣቢያዎች መካከል በማክሰኚት ወረዳ የሚገኘው የጤና ጣቢያ በበዓሉ ተሣታፊዎች ተጐብኝቷል፡፡ በዚሁ ወቅም UNFPA Ethiopia የተባለው ድርጅት የልብስ ማጠቢያ ማሽን ለማዕከሉ በእርዳታ አበርክቷል፡፡ ማዕከሉ ለህሙማኑ የህክምና አገልግሎት ከመስጠት ባሻገር የጥናትና የምርምር ሥራዎችን ይሰራል፡፡

ሙያተኞችን ማሰልጠንና ማብቃትም በማዕከሉ ውስጥ ከሚከናወኑ ተግባራት መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ በዓለም ላይ ከ2 ሚሊዮን የሚበልጡ ሴቶች በወሊድ ወቅት ለሚያጋጥም የፌስቱላ ችግር የሚጋለጡ ሲሆን በየዓመቱም 100ሺ የሚደርሱ ሴቶች የችግሩ ሰለባ ይሆናሉ፡፡ በአገራችን በየአመቱ ዘጠኝ ሺህ ሴቶች የፌስቱላ ችግር የሚያጋጥማቸው ሲሆን ወደ ህክምና ተቋማት በመሄድ ለችግራቸው መፍትሔ ያገኙት ግን 1200 የሚሆኑት ብቻ መሆናቸውም በዚሁ ወቅት ተገልጿል፡፡ ይህንን ችግር ለመቅረፍና መሠረታዊ የሆነ ለውጥ ለማምጣት ህብረተሰቡን ማስተማርና ያለ ዕድሜ የሚደረግ ጋብቻን ማስቀረት ጊዜ ሊሰጠው የማይገባ ተግባር መሆን እንዳለበት የበዓሉ ተሳታፊዎች ተናግረዋል፡፡ ያለ ዕድሜ ጋብቻ መዘዙ እጅግ የከፋ ነውና፡፡

Published in ዋናው ጤና

እንደ ዓለት የጸና ታሪክ፣ እንደ ፏፏቴ የሚፈስስ ዜማ የሚያፈስሱ ከንፈሮች፣ የልብ አፍንጫ የሚነቀንቅ የፍቅር መዓዛ ያለውን የኢትዮጵያ ሶማሌ ህዝብ ለመጎብኘት ወደ ኦጋዴን ስንበርር፣ አውሮፕላኑ በሁለት ክንፎቹ ሲበር፣እኛም ሺህ ክንፎች ያወጡ ልቦች ነበሩን፡፡ ኦጋዴን ገብተን ፈንጂ አየር ላይ ከነወንበራችን ሲያንሳፍፈን፣ኦብነግ መንገድ ላይ ቆርጦ ሲማርከን…እና ሌሎችም ሃሳቦች ነበሩብን፡፡ ኋላ እንደሰማሁት ብዙዎቻችን በዚህ ቅዠት ውስጥ ነበርን። ደሞ ታሪክ የማወቅ ጉጉትም አድሮብናል፡፡ በተለይ የኢትዮጵያ ሶማሌዎች፤ ውሳኔ ህዝብ የሰጡበትን ታሪካዊ ቦታ ማየት፡፡ አውሮፕላኑ ሲበርር እኔ አጠገብ ከተቀመጡት የአማራ መገናኛ ብዙሃን ሃላፊ ጋር ጥቂት አወራን፡፡ እኔ የነበርኩበት አውሮፕላን የመጀመሪያው ዙር በራሪ ሲሆን የኢፌዴሪ ፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አቶ ካሳ ተክለብርሃንም ነበሩና እያንዳንዳችንን በየመቀመጫችን እየመጡ ሰላምታ ሰጡን፡፡

አፈ ጉባዔው ከሰው ጋር ያላቸው ቅርርብ አስደማሚ ነው፡፡ ጎዴ ስንደርስ የኢትዮጵያ ሶማሌ ሰማይ፣ በጥቁር አድማሳት አይኖቹን ኩሎ ነበር የጠበቀን። ከአውሮፕላን ስንወርድ ህዝቡ የናፍቆት ዓይኖቹን እንደ ችቦ እያበራ…እንደወንዝ በሚፈስስ ዜማ…እንደ ቄጠማ እየተወዛወዘ ተቀበለን፡፡ እኛም ሲቃ በተሞላ ደስታ እጆቻችንን እያውለበለብን አጸፌታውን መለስን፡፡ እውነትም የኢትዮጵያ ሶማሌ ፍቅር ነው። እውነትም ይወዱናል፡፡ በአይኖቻቸው ላይ ያነበብነው ፍቅር ሌላ ፍቅር በልባችን ወልዶ ብዙዎቻችን በተመስጦ ውስጥ ወደቅን፡፡ “ይህን ህዝብ ለምን በኪናዊ ስራዎቻችን አላየነውም

” በሚል ራሳችንን ወቀስን፡፡ ሰዓሊው እጁ ነደደ፤ደራሲው በአርምሞ ውስጡ ታመመ፤ሙዚቀኛው ነፍሱ ታመሰች፡፡ የሁሉም ልብ በየመስመሩ ፈሰሰ። የሁሉም ሰው ነፍስ በኢትዮጵያ ሶማሌዎች ፍቅር ተጎረሰ፡፡ ሶማሌ የሚለው መጠሪያ “ሶሜ” በሚል ቁልምጫ እስኪለወጥ የከያኒውን ልብ ወሰዱት፡፡ በመጀመሪያው ቀን የጎዴ አዳር ብዙዎቻችን ፈራን፤ በተለይ እባብና ጊንጡን፡፡ ከፊላችን ያደርነው ቴክኒክ ኮሌጅ ውስጥ ነበር፡፡ በተለይ ለተጓዡ ሁሉ የሳቅ ምንጭ ከነበረው ሽመልስ አበራ (ጆሮ) ጋር ልዩ ጊዜ አሳልፈናል። ጊንጥና ጃርት የየራሳቸው ታሪክ ነበራቸውና ሰው በሳቅ አልቆ ነበር፡፡ ያ ብቻ አይደለም፤ ከዚህ ቀደም በተለያዩ ፕሮግራሞችና የጥበብ ዝግጅቶች የሚታወሱ አስቂኝ ነገሮች በሙሉ ተዘርግፈዋል፡፡ ሽሜ ዋናው ኮሜዲያን ይሁን እንጂ ታገል ሰይፉና ሌሎቹም ማለፊያ መዝናኛ ፈጥረውልን ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ሶማሌ ዜማዎችን ሳንረሳ ነው ታዲያ፡፡ እነዚህ ሰዎች በሙዚቃቸው ሃይል የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤውን በተደጋጋሚ ከመቀመጫቸው አስነስተው አስጨፍረዋል፡፡

ትከሻ-ለትከሻ ገጥመው አብረው ጨፍረዋል፡፡ በጎዴው አዳራችን እባብና አይጥ ፈርተን አንዳንዶቻችን ፍራሾቻችንን ወደ መሃል ለመሳብ ሞክረናል፡፡ ታዲያ ሽመልስ አበራ በሳቅ ሆዳችንን እያቆሰለው ሸሽተን ወደመኝታችን ሄድን፡፡ ግና አላመለጥንም፤ እየተከተለ ኮረኮረን፡፡ ማምሻውን እንናፈስ ብለን ወደከተማ ስንወጣ ሰው ሁሉ ዝነኛ አርቲስቶችን በስማቸው ይጠራ ነበር። ሽመልስ አበራ፣ ጥላሁን ጉግሳና ሌሎቹ ከየአቅጣጫው ይጠሩ ነበር፡፡ እንደ አበበ ባልቻ መከራ ያየ፣ የተከበበና ፎቶ በመነሳት የተጨናነቀ ግን አልነበረም፡፡ ሁሉም ከተማ፣ ሁሉም ሰው ቀድሞ የሚጠይቀው አስናቀ መጥቷል እያለ ነው፡፡ እንዲያውም ደገሀቡር ከተማ ምሳ በልተን የቡና ወረፋ ስንጠብቅ፣ አንድ ጠንከር ያሉ አዛውንት እንዲህ አሉ፤ “ያ አስናቀ መጥቷል?” እኛም “አዎ መጥቷል” አልናቸው፡፡ ሰውየው ተቆጥተው “…እርሱ’ኮ ነው የድግሳችንን ወጥ ያሳረረብን… የ40 ቀን መታሰቢያ ድግሳችንን ያበላሸው!” አሉ፡፡ ስለሁኔታው ሌሎችን ጠየቅን “ሰው ለሰው በኢቴቪ ሲጀመር አስናቀ መጣ፣ አስናቀ መጣ!” ተብሎ ሴቶቹ ሁሉ ቴሌቪዥን ሊያዩ ወጡ፡፡

በዚህ መሃል ነው ወጡ አረረ የተባለው፡፡ ሰውየው ግን “ቆይ” ብለው እየዛቱ ወደ መሀል ከተማ ሄዱ፡፡ “አበበ ባልቻ እግዜር ይሁንህ!” አልን፡፡ በማግስቱ ጧት ወደ ታሪካዊቷ ከተማ ካሊ ነበር የተጓዝነው፡፡ እኛ መኪና ውስጥ ድምፃዊው ሞገስ ተካ፣ የሙዚቃ ሃያሲው ሠርፀ ፍሬስብሀት፣ ዲያቆን ዳንኤል ክብረትና ሁለት የአፋር ክልል፣ ሁለት የጋምቤላ ክልል ጋዜጠኞች አሉ፡፡ አልፎ-አልፎም ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ ተክለአረጋይ አብሮን ይሆናል፡፡ አርቲስት አለለኝም ብቅ-ጥልቅ ይላል፡፡ ካሊ ስንሄድ ትንሽ አቧራ ነገር ነበር፡፡ ይሁንና ታሪኩ ለብዙዎቻችን የሚያጓጓ ነው፡፡ ያ ቦታ የኢትዮጵያ ሶማሌዎች፤ “ውሳኔ ሕዝብ” የሰጡበት ነው፡፡ እንግሊዛዊያን የሀገር ሽማግሌዎችን ሰብስበው “ከኛ ጋር ትሆናላችሁ ወይስ ከኢትዮጵያ?” ብለው ምርጫ የሰጧቸው ቦታ ነበር፡፡ አንድ የጉዟችን አባል ሲናገር እንደሰማሁት፤ እንግሊዞች እሾህ ላይ ነጠላ አንጥፈው ነጠላውን እሾህ ሲነክሰው “ኢትዮጵያ ማለት እንዲህ ናት!” ብለው አስጠንቅቀዋቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሶማሌዎች ግን በዚያችው አደባባይ፣ ሰማይና መሬት እያዩ፣ ፀሐይ እየታዘበች፣ ቁጥቋጦው እያሸበሸበ “እኛ ኢትዮጵያዊያን ነበር፤ አሁንም ነን፣ ወደፊትም በኢትዮጵያዊነታችን እንዘልቃለን” በማለት ቁርጡን ተናገሩ፡፡ የኢትዮጵያ ሶማሌዎች ኢትዮጵያዊ የሆኑት በመወለድ ብቻ አይደለም፡፡ በምርጫም ነው፡፡ ምንም እንኳ ይህንን የጠራ ባህር ሕዝብ ታሪክ ለማበላሸት አፈር ቢበትኑም ዛሬም ግን ሕዝባችን ከማናችንም በተሻለ የሀገር ፍቅር በልቡ የሚነድድ፣ ነድዶም የማያባራ ሕዝብ ነው፡፡

ለዚህም ነበር እርጥብ ቅጠል ይዞ በፍቅር ነበልባል በታጀቡ አይኖቹ የተቀበለን፡፡ ከጐዴ ከወጣን በኋላ የደናን ከተማ ሕዝብ ግራና ቀኝ ተሰልፎ ነበር፡፡ ቀብሪደሀር ስንሄድ ወጣቶቹ በፉጨትና በአድናቆት ተቀበሉን፡፡ በሚገባ ባላጣራም አንድ ከሙቀቱ ጋር በቢራ ሞቅ ያለው አርቲስት “አምላኬ ሆይ! እንደታቦት በሕዝብ ታጅቤ በእልልታና በሆታ እሸኝ ዘንድ እኔ ማን ነኝ?” እያለ በአድናቆት ደረቱን ይደቃ ነበር፡፡ በዚህ ጉዞ የኔ ትዝታም ደማቅ ነው፡፡ ቀብሪደሀር ከተማ አንድ ሱቅ ገብቼ ደብተር ልገዛ ስል፤ ሻጩ ወጣ የያዝኩትን ብር ወደ እኔ ገፍቶ በነፃ ሊሰጠኝ ሲል ገፍቼ መለስኩለት። ቀጥሎም የታሸገ ለስላሳ መጠጥ ለመግዛት መቶ ብር የሰጠሁት መስሎኝ ሁለት መቶ ብር ሰጥቼው ኖሮ መቶ ብሩን ሲመልስልኝ አንጀቴ ተላወሰ፡፡ ወገኔ ባይሆን፣ ባይወድደኝ መች ይህን ያደርግልኝ ነበር? የሚለው ነገር ለሕዝቡ ያለኝን ፍቅርና ክብር ጨመረው። ታዲያ በየከተማው መሀመድ ጠዊል፣ ሀብተሚካል ደምሴ፣ ዘውዱ በቀለ (ወላይትኛ) በባህላዊ ዜማቸው ሕዝቡን እንደማዕበል ነቅንቀውታል፡፡ ቀብሪደሀር ስንገባ 12ኛ መተማ ክፍለ ጦር ግቢ ነበር የተስተናገድነው። የሠራዊቱ አባላት ዳስ ተክለውልን በሚደንቅ መስተንግዶ፣ በሀገራዊ ፍቅር የምንገባበት እስኪጠፋን ተቀብለውናል፡፡ ይህ ክፍለ ጦር ግቢ፣ በገበየሁ አየለ “ጣምራ ጦር” መፅሐፍ ውስጥ የተጠቀሰ ሲሆን በየመንገዱ ያየናቸው ኩይሳዎች፣ መንገዶችና መልከዐ ምድራዊ አቀማመጦች ሁሉ ወደኋላ መለስ ብለን ገፆቹን በትዝታ እንድንገልጥ አድርገውናል፡፡

ከከተማ ወጥተን ደገሀቡር ስንገባ፣ የደገሀቡር ሕዝብም በሚገርም ሁኔታ ተቀበለን፡፡ መቼም ደገሀቡር የሸጋዎች ሀገር ናት፡፡ እንደ ቄጠማ የሚወዛወዙ ቆነጃጅት ነበሩ፣ ጣፋጭ ዜማ የሚያሰሙት፡፡ ወንዶችም ቁመናቸው የሚያምር፣ ፈገግታቸው ልብ የሚነካ ለዛ የተሞሉ ነበሩ፡፡ ታዲያ እዚህ ግቢ መኝታ ክፍሎች ስለነበሩ የቡድናችን አባል ሽመልስ አበራ ጡንቻም ስላለው ሁለት ክፍል ይዞ ጠበቀን፡፡ እኔ፣ ተስፋዬ ገ/ማርያም (ብሔራዊ ቴአትር) መልካሙ ዘሪሁን (ፀሐፌ ተውኔት) አንድ ክፍል፣ ውድነህ ክፍሌ፣ ታገል ሰይፉና ሽመልስ ከኛ ትይዩ ገቡ፡፡ የምሽቱን ደማቅ የበአል አከባበር ተቀላቅለን ተመልሰን ሻወር ከወሰድን በኋላ ወደየመኝታችን ገብተን ተኛን፡፡ ለካ ሦስት ሰዎች መኝታቸው ከመግባታቸው በፊት በአካባቢው ስለነበረው አራዊት ጠይቀዋል፡፡ የጠየቁት መኮንንም ምንም የሚያስፈራ ነገር እንደሌለ ይነግራቸዋል፡፡ ይሄን ብሎ ግን አላበቃም፡፡ “ብ…ቻ አንድ… ነገር አለ” አላቸው፡፡ ሳሚና ታገል ጆሮ ሰጡት። ተረከላቸው፡፡ “በአርጃም ይባላል፡፡ አዞ የመሰለ ሆኖ አራት እግሮች አሉት፤ ርዝመቱ ሁለት ሜትር ያህል ይሆናል፡፡ እንቅልፍ ካልወሰዳችሁ አይናካም፣ ግን ሰው እንቅልፍ እንዲወስደው የሚያደርግ መላ አለው - በፊት እግሮቹ ደባብሶ እንቅልፍ ያመጣል፡፡ አይናከስም፣ ብቻ ሁለት ምላሶች አሉት፤ እንቅልፍ የወሰደው ሰው ሲያገኝ ሁለቱን ምላሶቹን አፍንጫ ውስጥ ሰድዶ አንጐልን ይመጥጣል፡፡

ልክ ደም መምጣት ሲጀምር ግን ትቶ ይሄዳል” ይላቸዋል፡፡ ጭንቅ በጭንቅ እንደሆኑ ይመጣሉ፡፡ ሙቀት ስለነበር በረንዳ አንጥፈው ለመተኛት ቢፈልጉም “አርጃኖ” ትዝ ይላቸውና ወደ ክፍላቸው ይገባሉ፡፡ ክፍላቸው ሲገቡ የሆነች ተባይ ታሳድዳቸውና መኝታ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ይሄኔ የመኪናው ረዳት ወደ መግቢያው ላይ፣ ቀጥሎ ታገል ሰይፉ፣ ከዚያ ውድነህና ሽመልስ በተከታታይ ይተኛሉ፡፡ ታገል ጧት እንደነገረን፤ ከውጭ ንፋስ ሲያንቋቋ እርሱ አርጃኖን ያስባል፤ ተኝቼ እያለ አንጐሌን ይመጠው ይሆን? ሲል ያስብና “አይ ከኔ ቀድሞ ረዳቱ ስላለ እርሱን ሲገድል እሰማለሁ!” እያለ ሲያብላላ ይነጋል፡፡ ሽመልስ አድምቆ ያወራልን ሌላው ወሬ አብረን የሰማነው የአለምዬ ሶራ ዘፈን ተወዛዋዥ ነው። የሰቆጣው ልጅ ግንባሩ ላይ ትልቅ መስመር ነገር ጠባሳ ሆኖ ቀርቷል፡፡ ስለዚያ ሲተርክልን ከነብር ጋር ተናንቆ ታግሎ በመጨረሻው ነብሩን እንደገደለው ሲነግረን፣ ሁላችንም በግርምት ፈዝዘን ነበር፡፡ በማግስቱ ግን ሽሜ ምርጥ አድርጐ ተወነበት፡፡ ያ ሁሉ በመቀመጫው የፈሰሰ አርቲስት፣ ሆዱን እየያዘ ሳቀ፡፡ ሽሜ ምርጥ ኮሚዲያን ሆኖ ነበር፡፡

በዚህ ሁሉ ውስጥ ታዲያ የኢትዮጵያ ሶማሌዎች ፍቅር የሚረሳ አልነበረም፡፡ ሁላችንም ይህ ሕዝብ ፍቅር ነው! ውለታ አበዛብን! ፎንቃ አስያዘን እያልን ተገረምን። አትታዘቡኝና እኔ አሁን የኢትዮጵያ ሶማሌዎችን ሳይ እቅፍ አድርገህ “ሳማቸው ሳማቸው” ያሰኘኛል፡፡ እኔ ብቻ አይደለሁም፤ አጠገቤ የነበሩት ሁሉ ከጅጅጋ ስንወጣ በስደት ወደሌላ ሀገር እንደምንሄድ ተሰምቶን ነበር፡፡ ያ ፈገግታ… ያ… ዜማ… ያ ፍቅር እንዴት ሊረሳ ይችላል? በምን? ናፈቁን! ጅጅጋ ከተማ ገብተን በመጨረሻው ቀን መስተንግዶ ላይ የተሰማንን ገለጥን፣ ግጥሞች አቀረብን፣ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት እጅግ ውብ የሆነ ወግ አቀረበልን! …እያጣፈጠ አሳቀን፡፡ ጅጅጋ፣ የክልሉ እንግዶች ማረፊያ (Guest house) ግቢ ውስጥ ሦስት ነብሮች ታስረው ነበር። ታዲያ እነዚህን ነብሮች ያየ ሁሉ አብሯቸው ፎቶ መነሳት፣ ቪዲዮ መቅረፅ ጀመረ፡፡ ታገል ሰይፉ የአንዱን ነብር አንገት ደባበሰ፣ ሌሎችም አብረውት ፎቶግራፍ ተነሱ፡፡

ፀሐፌ ተውኔቱ ውድነህ ክፍሌ ግን ከሌሎች የተለየ እጣ ደረሰው፡፡ ነብሩ ሳያስበው ሁለት እጁን ቧጠጠው፡፡ ይሁን እንጂ በራሱ አንደበት እንደገለጠው፤ በሚያስደንቅ ጥበብና ስትራቴጂ ተጠቅሞ ራሱን አዳነ፡፡ ይህም በሳቅና ፌሽታ ተመንዝሮ ተሳቀበት፡፡ በጅጅጋ የማይረሳው ነገር ቢኖር የኢትዮጵያ ሶማሌ ፕሬዚደንት ንግግር ነበር። ሰውየው የማይቀመሱ እሳት፣ የሚጥሙ ጣፋጭ፣ የሚያስቁ ኮሜዲያን ነገር ናቸው፡፡ በመጨረሻው ቀን ስንብት አዳራሽ በገባን ቀን ሰውየው ንግግር ሊያደርጉ ነው ሲባል ሁላችንም ፈራን። አሰልቺ ንግግር ይሆናል ብለን ሃሞታችን ፈሰሰ። እንዳሰብነው ግን አልሆኑም፡፡ ያገር አርቲስት ልቡ እስኪፈርስ እየሳቀ እርስ በርስ እየተያየ፣ እጁ እስኪቃጠል እያጨበጨበ፣ ስብሰባው ተፈፀመ፡፡ የመጨረሻው ጭብጨባ ድምፅም እስካሁን በውስጤ ያስተጋባል። ሰውየው የዋዛ አይደሉም፤ አሁን ያለውን የኢትዮጵያ ሶማሌ መልክ ለማምጣትም ዋነኛው ተዋናይ፣ ደማቁ ቀለም እርሳቸው ናቸው ይባላል፡፡ ጉዟችን ወደ ሐረር ሲቀጥል የአቀባበል ውበት፣ የዜማው ሃይል የፈገግታው አቅም እየቀነሰ ሄዷል፡፡ ብዙ ነገሮች እየተዝረከረኩ አሰልቺ እየሆኑ መጡ፡፡ አብረውን የነበሩ ታዋቂ ሰዎች እጃቸውን እያነሱ ትርኪ ምርኪውን ሲያወሩ የብዙዎችንን ልብ ሰበሩት፡፡ መታወቅና ማወቅ ይለያያልና! ብዙ ዘባርቀው አንገታችንን አስደፉን፡፡ ጥሎ የማይጥል አምላክ፣ ሰርፀ ፍሬ ሰንበትን አስነስቶ “ኧረ እንደዚህ ብቻ አይደሉም፤ እንደዚህም ናቸው” የሚያሰኝ ምርጥ ሀሳብ፣ በሳይንስ የተደገፈ ጥበብ አወራ፡፡ ስለ አርአያነትም ረገጥ አድርጐ ገሰፀ፡፡ ቴዎድሮስ ተክለአረጋይም “ማሳሰቢያ” ብሎ በድሬዳዋው አዳራሽ አፈጉባኤው በተገኙበት አፋቸው እንዳመጣላቸው የሚናገሩ ሰዎችን አደብ ግዙ አለ፡፡ ድሬዳዋ ከተማ ሌላው ያየነው ነገር ሕፃናት ተሰብስበው ጥላሁን ጉግሳን “ዘሩ…ዘሩ…ዘሩ!” እያሉ ሲከብቡት ነው፡፡

መሄጃ ከልክለውት ነበር፡፡ ሳላጋንን ፖሊሶች ልጆችን እስኪለከልሉ ደርሷል፡፡ ይህ ነገር ያሳየኝ ልጆች የእሱን “ቤቶች” ድራማ የሚመለከቱት ከሆነ ለቀጣዩ ትውልድ መልካም ዘር መዝራት እንደሚገባው ነው፡፡ በመጨረሻው የጅጅጋ ሽኝት ቀንም ዘነበ ወላ፣ ሠራዊት ፍቅሬ፣ ሰርፀ ፍሬሰንበት፣ ዳንኤል ወርቁ፣ ንግግር አድርገዋል፡፡ ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራና እንዳለ ጌታ ከበደ ግጥም ያቀረቡ ሲሆን ዲያቆን ዳንኤል ክብረትም ምርጥ ወግ አቅርቧል፡፡ ደስ የሚሉ ቀናት አሳልፈናል፡፡ በትዝታ የሚታተሙ ዜማዎች አድምጠናል፡፡ ስቀጥል ፍቅር ወድቀናል ኢትዮጵያ ሶማሌ ፍቅር ነው ብለናል፡፡ ለሴት ልጆች ባላቸውም ክብር ተደምመናል ሴት ክቡር ናት!

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 15 June 2013 10:51

‘መኝታ’ እና ‘ቀለብ’…

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

ስሙኝማ…አዲስ አበባ ውስጥ በብዙ አቅጣጫ መንቀሳቀስ እንዲህ አስቸጋሪ ይሁን! የምር ግን…በተለይ የመኪናውን ትርምስ ያባባሰው ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…ሁላችንም መንገዱን በሊዝ የተኮናተርነው ይመስል ‘ቀድመን ማለፍ’ ስለምንፈልግ ይመስለኛል፡፡ ልክ እኮ…አለ አይደል… ቀድሞ ያለፈው ሰው የሆነ ቦታ “ማሰሮ ወርቅ ይጠብቀዋል…” የሚል መመሪያ ነገር የወጣ ነው የሚመስለው፡፡ ከተማዋ በአብዛኛው የእሽቅድድም ሜዳ ሆናለች! ግለኝነታችን በዛ!… በጣም በዛ!… እጅግ በጣም በዛ! ኮሚኩ ነገር ምን መሰላችሁ…ትራፊክ ፖሊሶች እያስተናበሩ እንኳን ለመሽቀዳደም መሞከር ምን ይባላል! በዚች እንኳን “አንተ ትብስ/ አንቺ ትብሽ” መባባል ሲያቅተን…ያሳዝናል፡፡ አለ አይደል…በአንዲት ስኩዌር ሜትር አስፋልት ላይ አምስት ሆነን ‘እኔ እቀድም፣ እኔ’ እየተባባልን እንዴት ነው የእውነት ከልባችን ለአገር የጋራ ህልም የሚኖረን! ደጉን ያምጣልንማ! እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… የህልም ነገር ካነሳን አይቀር… ይቺን አንድ ወዳጄ ሰብሰብ ብለን ሳለ ያጫወተንን ስሙኝማ…ሰውየው ህልም በጣም አስቸግሮት ሲገላበጥ ነው የሚያድረው፡፡ እናላችሁ…መፍትሄ ባገኝ ብሎ አንድ የሚያውቃቸው ቄስ ዘንድ ይሄዳል፡፡

ለእሳቸውም “አባ ህልም አስቸገረኝ፣ ሰላማዊ እንቅልፍ መተኛት አልቻልኩም፣” ይላቸዋል፡፡ እሳቸውም “ለመሆኑ ምን አይነት ህልም ነው የምታየው?” ይሉታል፡፡ እሱም… “በቃ፣ የሆነ በሬ እንዲሁ አገር ለአገር ሲያሳድደኝ ነው የሚያድረው” ይላቸዋል፡፡ እሳቸውም “ያው ሁላችንስ ህልም እናይ የለ፣ ግዴለም ይተውሀል፡፡ ደግሞ ሌላ ቀን ሌላ አይነት ህልም ታያለህ” ይሉታል። እሱም “ኧረ አባ… ይኸው በሬ በየዕለቱ አልለቀኝ ብሎ ሲያሳድደኝ ስንት ሳምንቴ!” ይላል፡፡ ይሄኔ ቄሱ “ለመሆኑ ምን ላይ ነው የምትተኛው?” ብለው ይጠይቁታል፡፡ እሱም “ሳር ፍራሽ ላይ…” ሲል መለሰላቸው፡፡

ይሄኔ ቄሱ ምን ቢሉ ጥሩ ነው…“ታዲያ በሬውስ ቢሆን ምን ያድርግ… ቀለቡ ላይ ነው እኮ የተኛህበት…” አሉት አሉ፡፡ (ወዳጄ ስለ ‘ኮፒራይቱ’ በኋላ እንነጋገራለን፡፡) እና ዘንድሮ ብዙ ነገሮች ቀለባችን ላይ ተኝተውብን…ወይ ማንቀሳቀስ አንችል፣ ወይ ራሳቸው አይንቀሳቀሱ! መሥራት የምትችሉትን ነገር ሁሉ በተለያየ ምክንያት መሥራት እንዳትችሉ ስትሆኑ… ቀለባችሁ ላይ ተተኝቶበታል ማለት ነው! ሙሉ አቅማችሁን ተጠቅማችሁ እንዳትሠሩ የቃልና የጽሁፍ መመሪያዎች፣ ሰርኩላሮች ‘የኮሚቴ ውሳኔዎች’ ምናምን እንቅፋት ሲሆኑባችሁ…ቀለባችሁ ላይ ተተኝቶበታል ማለት ነው! በአለቃነት ሰፊ ወንበር ላይ ተቀምጠው (‘ተኝተው’ የሚለውም አማራጭ ሊሆን ይችላል) እንደ ፈረስ ልጓም ካላገባሁልህ፣ እንደ በቅሎ ካልተቀመጥሁህ... ምናምን ሲሏችሁ ቀለባችሁ ላይ ተተኝቶበታል ማለት ነው! ዕውቀቱና ችሎታው ሳያንሳችሁ የሚገባችሁን ቦታ በ‘ቦተሊካ’ ወገንተኝነት ወይም በ‘አገር ልጅነት’ እንድታጡት ሲደረግ… ቀለባችሁ ላይ ተተኝቶበታል ማለት ነው! ቀን ተሌት እየፈጋችሁ በኦፊሴላዊ ወረቀቶችና ኦፊሴላዊ ባልሆኑ የመጋረጃ ጀርባ ሹልክልኮች የሚገባችሁን ዕድገትና የተሻለ ቦታ እንዳታገኙ ስትደረጉ…ቀለባችሁ ላይ ተተኝቶበታል ማለት ነው! እናላችሁ…እንዲህ፣ እንዲህ ቀለቦቻችን ላይ የተኙ ነገሮች መአት ናቸው፡፡

(በሬውስ ቢያንስ፣ ቢያንስ ቀለቡን ነጻ ለማውጣት በ‘ህልም’ እንኳን መጥቶ ያሳድዳል፡፡ እኛ አለን እንጂ…አለ አይደል…ሥጋዊና መንፈሳዊ ‘ቀለቦቻችን’ ላይ ተተኝቶባቸው እኛም ለሽ ብለን አብረን የተኛን!) ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ጥያቄ አለን… ይሄ ሰውየውን በህልሙ እያሳደደ ያስቸገረው በሬ…አንድ ጊዜ መንገድ ላይ እየተነዳ ሲሄድ ሳለ አልሄድም ብሎ ለግሞ በጆሮው “እንትን መጣልህ!” ሲሉት በአራት ሳይሆን በአሥራ አራት እግሩ ‘ያቀጠነው’ በሬ ይሆን እንዴ! ልክ ነዋ…ዘንድሮ እኮ በአንደኛው በር ወጥቶ “ላይመለስ ዓለም ዳርቻ ሄዷል” ያላችሁት በሌላ በር ተመልሶ ከች ይልላችኋል፡፡ የህልም ነገር ካነሳን አይቀር…ይቺን ስሙኝ…ሚስት ሆዬ ጧት ከእንቅልፏ ስትነቃ ለባሏ… “ዛሬ እንዴት አይነት ቆንጆ ህልም አየሁ መሰለህ…” አለችው፡፡ ባል ምን አየሽ አላት፡ ሚስትም ምን የመሰለ ሀያ አራት ካራት፣ ሠላሳ አምስት ግራም የወርቅ ሀብል በስጦታ ስትሰጠኝ አየሁ፡፡

ትርጉሙ ምን ይመስልሀል?” ስትል ጠየቀችው፡፡ ባልም “ማታ መልሱን ታገኚዋለሽ…” አላት፡፡ ማታ ሲመጣም የሆነ ነገር በአሪፍ የስጦታ ወረቀት የተጠቀለለ ነገር ይዟል፡፡ ሚስትም በደስታ ተጠመጠመችበት። እየተፍነከነከች የተጠቀለለበትን ወረቀት ስትከፍተው ምን አገኘች መሰላችሁ…‘የህልም አተረጓጎም’ የሚል መጽሐፍ! እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ፣ ሳልረሳው… ጥያቄ አለን፤ በቃ የፈርኦን ሰዎች “ካልሆነማ…” ምናምን አይነት የተዘዋዋሪ “ነብር አየኝ በሉ!” ምናምን ሲሉ…አለ አይደል…ነገርዬው “ቀጥኜ ቢያየኝ ጅማት ለመነኝ!” ምናምን አይነት መሰለ እኮ! አሀ…ቢሆንም ባይሆንም “አይ አልበዛም! በአባቱ ባድማ የተኛውን በሬ ባትነካኩት ይሻላችኋል…” አይነት ነገር ማለት ያስፈልጋላ! የጣይቱ “ከፈለግህ ዛሬውኑ አድርገው…” ይሄኔ ነበር! ነው… ወይስ ወዳጃችን “እመሃል ገብታ በለው…” የምትለውም፣ ወዳጃችን አፋፍ ቆማ “ተው ሽሽ…” የምትለውም ተቀላቅለን ያረፍን መሰላቸው! ነገርዬው…አለ አይደል…‘ቁርበት ምን ያጓጓሀል ቢሉት ባያድለኝ ነው እንጂ የነጋሪት ወንድም ነበርኩ አለ’ አይነት እንዳይሆን፡፡

(ደግሞም…አንዳንድ ‘ቦሶቻችን’ መፎከር ‘እኛ’ ላይ ብቻ አይደለም! “ማንን ታሸንፋለህ ቢሉት ሚስቴን አለ…” የሚለው አባባል ለምን ትዝ እንዳለኝ ለማወቅ እየሞከርኩ ነው! ቂ…ቂ…ቂ…) ልጄ ሰዎቹ ካሜራ እያለ እንደዛ ከተለፋለፉ፣ ብቻቸውን ሲሆኑማ የማይሉን አይኖርም ማለት ነው፡፡ ስሙኝማ…ምን ያሳዝንሀል አትሉኝም፣ ምናልባት ሊሆን የማይችል ቢሆንም ወይም የመከሰቱ ነገር በጣም የጠበበ መሆኑም ጦርነት የሚለው ቃለ ዕለታዊ መዝገበ ቃላታችን ውስጥ እንደገና ‘ሾልኮ መግባቱ’ አያሳዝናችሁም? የእኛ የማዳመጫ ህዋሳት በጎ፣ በጎ ነገር ሳይጠግቡ ሌላ ሚሌኒየም ሊደርስ ነው! አንድዬ ብቻ ሁሉንም ያስተካክለው! እኔ የምለው…የተለያዩ ሚዲያዎችን ስትሰሙ ደግሞ አንዳንዴ የሚሰጡት ማብራሪያዎች ‘የተሳሳተ’ ከመባል ይልቅ ‘ውሸት’ ወደ መሆን ይጠጋሉ፡፡ እናማ… ግጥምና መዝሙር ብቻ ሳይሆን “እንዲህ በአደባባይማ እንደልባችሁ ስትዋሹ ዝም አንልም…” ማለት ያስፈልጋል፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…አንድ ሰውዬ ማንም ሰው ውሸት በሚናገርበት ጊዜ በጥፊ የሚያጮል መሣሪያ ይፈለስፋል፡፡

ማታ ሰውየው፡— ሚስቱና ወንድ ልጃቸው ለእራት ይቀመጣሉ፡፡ አባት፡— ጎረምሳው፣ ዛሬ በትምህርት ሰዓት የት ነበርክ? ልጅ፡— ትምህርት ቤት (መሣሪያው በጥፊ አጮለው) አይ፣ ሲኒማ ገብቼ ነበር፡፡ ምን ፊልም አየህ? ልጅ፡— ሃሪ ፖተርን (መሣሪያው በጥፊ አጮለው) አይ፣ የወሲብ ፊልም ነው ያያሁት፡፡ አባት፡— ምን! እኔ በአንተ ዕድሜ በነበርኩበት ጊዜ የወሲብ ፊልም አይቼ አላውቅም (መሣሪያው በጥፊ አጮለው) ሚስት፡— ምንም ቢሆን የአንተ ልጅ ነው፡፡ (መሣሪያው ደህና አድርጎ በጥፊ አጮላታ!) ስሙኝማ…የህልም ነገር አንስተን የለ…ይቺን ስሙኝማ፡፡ ሰውየው አሉ ብዙ ጊዜ በህልሙ የሚያየው ጓደኞቹን ብቻ ነው፡፡ እንደውም በእውኑ ከሚያገኛቸው ጓደኞቹ በህልሙ የሚያገኛቸው ይበዛሉ! ታዲያላችሁ… ማንኛውንም ጓደኛውን በህልሙ ባየ ቁጥር ድምጹን ከፍ አድርጎ “ሄሎ!” ይላል፡፡ ሚስት ደግሞ እሱ በጮኸ ቁጥር እየባነነች ተቸግራለች፡፡

እናማ…ነገርየው ስልችት ያላት ሚስት አንድ ቀን ማታ ምን አለችው መሰላችሁ… “ዛሬ ድንገት በህልምህ የሆነ ጓደኛህን ካገኘህ እባክህ እጅህን አወዛውዘህ ብቻ ሰላም በለው፡፡” አሪፍ አይደል! እናላችሁ…በሬው ቀለብ ላይ እንደተኛው ሰው ቀለባችን ላይ ‘የተኙብን’ መአት ነገሮች አሉ፡፡ ከአስተሳብና አመለካከት ጀምሮ እስከ ግለኝነትና ፍጥጥ ያለ ክፋት ድረስ… ቀለባችን ላይ የተኙ ነገሮች ተቆጥረው አያልቁም፡፡ አንድ በአንድም፣ በጅምላም ቀለባችን ላይ ያለ ቀስቃሽ ‘ለሽ ያሉትን’ ነገሮች የሚያነሳልንን ተአምር አንድዬ ይላክልንማ! ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል
Saturday, 15 June 2013 10:47

ወደ ምስራቅ ተመልከቱ!

የዛሬ ሁለት ሳምንት 200 የሚደርሱ አባላት የተካተቱበት እውቅ የኪነጥበብ ባለሙያዎች፣ ጋዜጠኞችና የፖለቲከኞች ቡድን፤ በፌዴሬሽን ምክር ቤትና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልላዊ መንግስት አስተባባሪነት “የምስራቅ ኢትዮጵያን እንወቅ” በሚል መርህ የሶማሌ፣ የሃረሪ ክልል እና የድሬዳዋ መስተዳድርን ጐብኝተዋል፡፡ በዚህ ፅሁፌ በጉብኝቱ ወቅት ይፋ ስለተደረጉ አንኳር ፍሬ ጉዳዮች የማስቃኛችሁ ሲሆን ፅሁፌን የምጀምረውም የሱማሌ ህዝብ እንዴትና ለምን ኢትዮጵያዊ ሆነ ከሚለው ነው፡፡

አፍሪካን በቅኝ ግዛት በመቀራመት እንግሊዝ እና ፈረንሣይ ትልቁን ስፍራ ይይዛሉ፡፡ በምስራቅ አፍሪካ ላይ አንዣብባ የነበረችው ጣሊያንም ተጠቃሽ ናት፡፡ እነዚህ ሶስት ሃገሮች የዛሬዋን ሶማሊያ በመቀራመት የኢጣሊያ ሶማሌ፣ የእንግሊዝ ሶማሌ እና የፈረንሣይ ሶማሌ (ጅቡቲ) እያሉ ያስተዳድሩ ነበር፡፡ በወቅቱ በኢትዮጵያ ግዛት ውስጥ ይገኙ የነበሩ የሶማሌ ጐሣ አባላትንም በተለይ እንግሊዞች ድንበር ጥሠው እየገቡ አስተዳድረዋል፡፡ ለአካባቢው ማህበረሠብ ከማዕከላዊው የኢትዮጵያ መንግስት የተሠጠው ትኩረት እምብዛም በመሆኑም እንግሊዞች በአካባቢው የሶማሌ ተወላጆች ላይ የተለያዩ ጫናዎችን ያደርጉ ነበር፡፡

የተለያዩ እርዳታዎችንና እጅ መንሻዎችን በማቅረብም በማህበረሠቡ ዘንድ ትልቅ ተሠሚነት ያላቸውን የጐሣ መሪዎች እየሠበሠቡ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ክህደት ፈፅመው አብረዋቸው እንዲያብሩ ይገፏፏቸው ነበር፡፡ እንዲያውም የኢትዮጵያን መንግስት ትተው በእነሡ አስተዳደር ስር እንዲጠቃለሉ ይወተውቷቸው ነበር፡፡ የሃገር ሽማግሌዎችና የጐሣ አባላትን እየሠበሠቡ፣ ከኢትዮጵያ መንግስት “ቅኝ አገዛዝ” ይልቅ የእንግሊዝ መንግስትን አስተዳደር በመምረጥ የአውሮፓዊ ስልጣኔ ተቋዳሽ ሲሆኑ በተደጋጋሚ መክረዋቸዋል፡፡ ይህን ተደጋጋሚ ውይይት የሚያደርጉት ደግሞ የክልሉ እምብርት በሆነው ለኦጋዴን አካባቢ በመገናኘት ነው፡፡ አሁን ያለው የክልሉ መንግስት ለጉብኝቱ አባላት ስለዚህ ታሪካዊ ሂደት ገለፃ አድርጓል፡፡

ለ“ኢትዮጵያ” ሶማሌዎች የእንግሊዝ መንግስት በተደጋጋሚ የሚያቀርበው የእኔ ግዛት አካል ሁኑ ጥያቄ ለመጨረሻ ጊዜ እልባት ያገኘው ዛሬ በሸበሌ ዞን በደናን ወረዳ ውስጥ በምትገኘው “ካሊ” በተባለች ስፍራ ነው፡፡ በወቅቱ ተልዕኮ የተሠጣቸው የእንግሊዝ መንግስት ተወካዮች ካሊ በመገኘት የሃገር ሽማግሌዎችን ሠበሠቡ፡፡ ሽማግሌዎቹንም ወይ እንግሊዝን ወይ ኢትዮጵያን እንዲመርጡና ቁርጠኛ ውሣኔያቸውን እንዲያሣውቋቸው ጠየቁ፡፡ የሃገር ሽማግሌዎቹ ግን ከእንግሊዝ ይልቅ የኢትዮጵያ መንግስት ይሻለናል፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን እንጂ የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት አካል መሆን አንፈልግም ሲሉ በዚህች ታሪካዊ ቦታ ላይ አሣወቁ፡፡ ከዚያን ጊዜ በኋላም ሱማሌዎች በኢትዮጵያዊነት ፀኑ፡፡ በጉብኝቱ ወቅት ይህን ታሪክ ለትውልድ የማስተላለፍ ሃላፊነት የወሠዱት የሃገር ሽማግሌዎች ለጉብኝቱ አባላት እንደገለፁት፤ እንግሊዞች በዚህ ውሣኔ ተናደው ከአባባቢው ከመሄድ ባሻገር ይህ በሚስጥር ሲያደርጉት የነበረው ድርድር በማዕከላዊው የኢትዮጵያ መንግስት እንዳይሠማ ስጋት አድሮባቸው ነበረ፡፡

ምክንያቱም በወቅቱ ሃገሪቱ ከኢትዮጵያ ጋር በወዳጅነት ላይ የተመሠረተ ግንኙነት ነበራትና ነው፡፡ በእንዲህ ያለ መልኩ ኢትዮጵያዊነትን የመረጡት ሱማሌዎች፤ ከተቀሩት ሱማሌዎች ንቀትና ጥላቻን አትርፈዋል፡፡ ይህ እውነታም ለዘመናት ደብዝዞ እንዲቀር የእነዚህ ሃይሎች ሚና ቀላል እንዳልነበረ መረዳት ይቻላል፡፡ የኢትዮጵያ ሱማሌ ህዝብ ከእንግሊዝ የቀረበለትን የሪፈረንደም ምርጫ ኢትዮጵያዊነትን በመምረጥ ያጠናቀቀ መሆኑ በማዕከላዊው መንግስት የሚታወቅ ባለመሆኑ፣ ሁሌም በሃገር ክህደት ጥርጣሬ የሚታይ ነው፤ ይህም ሆኖ በአፄ ሃይለ ስላሴ ዘመን ሃገሪቱን ከቅኝ ግዛት ናፋቂዎች በምስራቅ በኩል በመከላከል በደጀንነት ሚናውን ተወጥቷል፡፡ “እኛ ኢትዮጵያውያን ነን” የሚለው ውሣኔ በሃገር ሽማግሌዎች ከተላለፈ በኋላ፣ በክልሉ ህዝብ ሌላ የታሪክ ምዕራፍ የተገለጠው የዚያድ ባሬ ጦር በ1968 መላዋን ኢትዮጵያ ለመውረር በተንቀሣቀሠበት ወቅትና ከዚያ በኋላ እስከዛሬ ድረስ ባለው ጊዜ ነው፡፡ ታላቋን ሱማሊያ የመመስረት አላማ አንግቦ የተነሣው ዚያድ ባሬ፤ በኢትዮጵያ የሚኖሩ ሱማሌዎችን፣ በጅቡቲ ያሉ ሶማሌዎችንና በእንግሊዝና በጣሊያን ስር የነበሩ ሶማሌዎችን አንድ በማድረግ ታላቋን ሶማሊያ እውን ማድረግ ቀዳሚው አላማ አድርጐ ተንቀሣቅሷል፡፡ የወረራው ቀዳሚ ሠለባ የኢትዮጵያ ህዝብ በመሆኑም በርካቶቹ ጦርነቱን ሽሽት ወደ ዋናዋ ሱማሊያ እንዲሸሹ ተደረገ፡፡

የክልሉ የአሁኑ ርዕሠ መስተዳደር አብዲ መሃመድ ለጉብኝቱ አባላት ጅጅጋ ከተማ ላይ ባቀረቡት የክልሉ ታሪካዊ ዳራን የዳሠሠ ጥናታዊ ፅሁፍ ላይ፤ በወቅቱ ጦርነቱን ሸሽተው ወደ ሱማሊያ በመሄድ በካምፕ ያረፉ ስደተኞችን እየመለመለ፣ ዚያድ ባሬ በፕሮፓጋንዳ ያጠምቅ ነበር፡፡ ስደተኞቹን የታላቋ ሱማሊያ አካል ናችሁና ሃገራችሁን ከደርግና ከኢትዮጵያ አገዛዝ ነፃ ማውጣት አለባችሁ ይል ነበር፡፡ ሃሣቡን የተቀበሉትንም እያሠለጠነ ለሃይል ፍልሚያው ዝግጁ እንዲሆኑ አስታጠቃቸው፡፡ ድጋፋቸውን ማግኘቱን ሲያረጋግጥም በኬንያ፣ በሞቃዲሾ፣ በጅቡቲና በኢትዮጵያ ያሉ ሱማሌዎችን አንድ አድርጌ ታላቋን ሶማሊያ እውን አደርጋለሁ የሚለው ህልሙ የሚሳካ መስሎት የመጀመሪያ ኢላማውን ሠፊውን የሱማሌ ህዝብ አቅፋ በምትገኘው ኢትዮጵያ ላይ አነጣጠረ፡፡ ለጊዜው የተሣካ የመሠለ ድልም በመቀናጀት መሃል ሃገር ድረስ ዘልቆ በመግባት ብዙ ውድመቶችን አደረሠ፡፡ በርካታ ኢትዮጵያውያን ሱማሌዎችንም በአስተሣሠቡ አጠመቀ፡፡ ጥቂት የማይባሉትም ከዚያድ ባሬ ጦር ጋር በማበር መልሠው ሃገራቸውን ወጉ፡፡ አብዛኛው በተለይም ይህን ኢትዮጵያዊ የመሆን የሪፈረንደም ውሣኔ ያፀደቁና ሚስጥሩን የሚውቁት ግን አሁንም የዚያድ ባሬን ወረራ ተቃወሙ፡፡

እንዲያም ሆኖ ለማህበረሠቡ የተሠጠው የኢትዮጵያዊነት ማዕረግ አነስተኛ እንደነበር አቶ አብዲ በጥናታቸው ጠቁመዋል፡፡ በወቅቱ ደርግ የሱማሌ ማህበረሠብን እንደ ሌላው ኢትዮጵያዊ አይመለከትም፡፡ “አንተ ሽርጣም ሡማሌ” ከሚለው ዘለፋ ጀምሮ በጥርጣሬ ይመለከት ነበር፡፡ በዚህም ሳቢያ አብዛኛው ማህበረሠብ በኢትዮጵያዊነት አስተሣሠብ የተቀረፀ አልነበረም። ደርግ እንዲህ በጥርጣሬ ማህበረሠቡን ሲመለከት ዚያድ ባሬ በበኩሉ፤ ከእሡ ጐን ቆመው የማይዋጉትን ያሠቃይ ነበር፡፡ በዚህ የተነሣ ህዝቡ ከሁለት ያጣ ሆኖ ለወራት በዘለቀው ጦርነት ብዙ ተጐድቷል፡፡ እንዲያውም ደርግ በዚያድ ባሬ ጦር ተሸንፎ ከቀብሪ ደሃር ለቆ በመውጣት ወደ ደጋሃ ቡር ሲገባ “አንተም ሱማሌ ያም ሱማሌ” እያለ በርካቶችን መጨፍጨፉን አቶ አብዲ በጥናታቸው ይገልፃሉ፡፡ ደርግም ዚያድ ባሬም የኢትዮጵያ ሱማሌን በእኩል ጨፍጭፈዋል፡፡ ደርግ በሃገር ክህደት እየወነጀለ ሲጨፈጭፍ፣ ዚያድ ባሬ ደግሞ አርፋችሁ ተገዙ በሚል ይጨፈጭፍ ነበር፡፡ ህዝቡም በአፀፋው ደርግን ከመውጋት ይልቅ ዚያድ ባሬን ነበር የሚፋለመው የሚሉት አቶ አብዲ፤ በትግሉ ሂደትም ዚያድ ባሬ የሾማቸው የወረዳ አመራሮች ላይ በድብቅ ጥቃት ይፈፅም ነበር፡፡ ለትዕዛዛቸውም ቀና ምላሽ አይሠጥም፡፡

በዚህም ብዙ የዚያድ ባሬ የሡማሊያ አመራሮች ተገድለዋል፡፡ በድርጊቱ የተናደደው ዚያድ ባሬም ጦሩ ተሸንፎ ከኢትዮጵያ ሲወጣ በመውጫ መንገዱ ያገኛቸውን ኢትዮጵያውያን ሱማሌዎችን ጨፍጭፏል፡፡ የታላቋ ሶማሊያ ጦር ሃገሪቱን ለቆ ቢወጣም በተለይ ኦጋዴን አካባቢ የተለያዩ ጥያቄዎች ይነሡ ነበር፡፡ እነዚህ ጥያቄዎች ደግሞ በኋላ ሃገሪቱን ከደርግ ተረክቦ ማስተዳደር በጀመረው የኢህአዴግ ስርአትም ተጠናክረው ቀጥለዋል፡፡ የክልሉ ህዝብ ሶስተኛው የታሪክ ምዕራፍ የሚጀምረው ኢህአዴግ ኢትዮጵያን ከተቆጣጠረበት ከ1983 ዓ.ም በኋላ ነው፡፡ በወቅቱ ራስን በራስ ማስተዳደር የሚለው ሃሣብ ሲመጣ እንደ ሌላው የኢትዮጵያ ክፍል ሁሉ የተማሩ የሚባሉ የማህበረሠቡ ተወላጆች ፓርቲ ማቋቋም ጀመሩ። 14 ድርጅቶችም ወዲያው ተመሠረቱ፡፡

እነዚህ ድርጅቶች መመስረታቸው ባልከፋ ነበር፤ ነገር ግን ሁሉም የተመሠረቱት በዚያድ ባሬ ጊዜ የኢትዮጵያ መንግስትን ሲወጉ በነበሩ ጀነራሎችና የጦር መኮንኖች ነበር፡፡ እነዚህ መኮንኖች ፓርቲዎቹን ሲመሠርቱም በጐሣቸው ተከፋፍለው ስለነበር የኋላ ኋላ ብዙ መዘዞችን አስከትሏል፡፡ በወቅቱ ፓርቲዎቹ የተለያየ ፍላጐት ይዘው ቢመሠረቱም ሁሉንም አንድ የሚያደርጋቸው አጀንዳ ግን ነበራቸው፡፡ ይኸውም የሶማሌ ክልልን ከኢትዮጵያ መገንጠል የሚለው ነው፡፡ አስራ ሶስቱ ድርጅቶች በኢትዮጵያ ያለውን የሶማሌ ማህበረሠብ ግዛት ይዘን ወደ ታላቋ ሶማሊያ እንቀላቀል ሲሉ፣ የኦጋዴ ብሄራዊ ነፃ አውጪ ግንባር (ኦብነግ) በበኩሉ፤ ከሶማሊያ ጋር ሣንቀላቀል የኦጋዴን ነፃ ግዛት (ሃገርን) መመሥረት አለብን አለ፡፡ ይህ ሁሉ የሃሣብ ፍጭት ሲካሄድ ምንም እንኳ ኢህአዴግ አዲስ አበባን የተቆጣጠረ ቢሆንም የደርግ አመራሮች በሱማሌ ክልል መደበኛ ስራቸው ላይ ነበሩ፡፡ አቶ አብዲ እንደሚሉት፤ በወቅቱ የነበሩት የደርግ አመራሮች ቦታውን ለሱማሌ ተወላጆች ሣያስረክቡ ትንሽ ስልጠና ተሠጥቷቸው ቢቆዩ ኖሮ፣ የኋላ ኋላ በክልሉ የተፈጠረው የፖለቲካ ቀውስ ባልተከሠተ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ኢህአዴግ ደርጐችን ከቦታው ሲያስለቅቅ ወዲያው የዚያድ ባሬ ጀነራሎች እና የደህንነት ሠዎች ነበሩ ቦታውን የተቆጣጠሩት። የመጀመሪያውን የክልሉን መንግስት ስልጣንም ኦብነግ ተቆጣጠረ፡፡

የተቀሩት 13 ድርጅቶችም በጐሣ ተሰባጥረው “ሊግ” የሚባል የጋራ ህብረት የፈጠሩ ቢሆንም ብዙም ሣይቆይ ሊፈርስ ችሏል፡፡ ኦብነግ ነፃይቱን ኦጋዴን ለመመስረት ይንቀሣቀስ እንጂ ዋነኛ የአስተሣሠብ ቅኝቱ የዚያድ ባሬ ነበር፡፡ ኢህአዴግ ስልጣን ላይ ሲወጣ ጀምሮ የኢትዮጵያን ባንዲራ፣ የህዝብ መዝሙር፣ መከላከያ የመሣሠሉትን ብሄራዊ መገለጫዎችን አይቀበልም ነበር፡፡ ይህ ሁኔታም ክልሉ እስከተረጋጋበት እስከ 2000 ዓ.ም ቀጥሎ መስተዋሉን አቶ አብዲ ይገልፃሉ፡፡ የክልሉ ብሄራዊ መዝሙር ቀደም ሲል ለታላቋ ሶማሊያ ሠንደቅ አላማ የተዘመረ ነበር፡፡ በፍሬ ሃሣቡም የኢትዮጵያ መንግስትን አጥብቆ የሚቃወም ነው፡፡ ይህ መዝሙር ሲዘመር በነበረበት ከ1983-2000 ዓ.ም በርካታ የፌደራል መንግስት ባለስልጣናት የመዝሙሩን ፍሬ ሃሣብ ሣይገነዘቡ አብረው ቆመው ዘምረዋል የሚሉት አቶ አብዲ፤ በኋላ እውነታው ወጥቶ ከኦብነግ ርዝራዦች ከክልሉ ተጠራርጐ መጥፋት ጋር አብሮ መክሠሙን አስረድተዋል። አሁን ስለ ክልሉ ተጨባጭ ሁኔታ የሚዘረዝረው መዝሙርም ከሚያዝያ 4 ቀን 2000 ዓ.ም ጀምሮ በስራ ላይ እንደዋለ ተመልክቷል፡፡ ክልሉን ከኦብነግ ይፋዊ “ፋኖ ተሠማራ” አዋጅ በኋላ ተረክቦ ሲያስተዳድር የነበረው የሶማሌ ዲሞክራቲክ ፓርቲ (ሶዴፓ)ም ከጐሣ አመለካከትና ከኦብነግ አስተሣሠብ የፀዳ አልነበረም፡፡ በውስጡ የነበሩ በርካታ አመራሮች በሁለት ቢላዋ የሚበሉ ነበሩ፡፡ በአንድ በኩል ህገመንግስቱን የተቀበሉ በማስመሠል ከፌደራል መንግስት ጋር ተባብረው ሲሠሩ፣ በሌላ በኩል ጫካ ለሚገኘው ኦብነግ ስንቅ በማቀበልና የጥቃት በሮችን በመክፈት ይተባበሩ ነበር፡፡

ከፌደራል መንግስት የሚላከው በጀት ሣይቀር ጫካ ለሚገኙት የኦብነግ ታጣቂዎች በደሞዝ መልክ ጫካ ድረስ ተወስዶላቸው ፈርመው ይቀበሉ ነበር፡፡ ይህ ደግሞ የኋላ ኋላ ኦብነግ እየተጠናከረ መጥቶ ራስ ምታት ለመሆን የመቻሉ ምስጢር አንዱ ምክንያት ነው፡፡ ኦብነግ እንዴት ተጠናከረ? በዘውዳዊው ስርአትና በደርግ ጊዜ የክልሉ ማህበረሠብ የሁለተኛ ዜግነት ማዕረግ እንዲኖረው መደረጉና ከሌላው የሃገሪቱ ማህበረሠብ የተለየ ተደርጐ መቆጠሩ፣ ህዝቡ ነፃ እናወጣሃለን ለሚሉት ልቡ እንዲያደላ አድርጓል፡፡ ኢህአዴግ ከመጣ በኋላም ይህ አስተሣሠብ ባለመቀየሩ የበለጠ ለኦብነግ ፕሮፓጋንዳ አመቺ ሆነ፡፡ ኦብነግ ለህዝቡ በሚያስተላልፋቸው መልዕክቶች “አማርኛ የሚናገር ደርግ ሄዶ ትግርኛ የሚናገር ደርግ መጣ” ይል ነበር፡፡ በዚህ የህዝቡን በተለይም በማህበረሠቡ ትልቅ ቦታ የሚሠጣቸውን የሃገር ሽማግሌዎችና የሃይማኖት መሪዎችን ቀልብ መግዛት ቻለ፡፡ ድጋፍም በሠፊው አገኘ፡፡ በትጥቅ፣ በኢኮኖሚ፣ በኔትወርክ (ግንኙነት) በደንብ ተጠናከረ፡፡ በርካታ የክልሉን ዞኖችና ወረዳዎችም በእጁ አስገብቶ ያስተዳድር ነበር፡፡

በጅጅጋ፣ በጐዴ ከሚገኙ አራት ካምፖች በስተቀር ሁሉም ወታደራዊ ካምፖች በቁጥጥሩ ስር ነበሩ - እስከ 2000 ዓ.ም ድረስ፡፡ ይህን እንቅስቃሴያቸውን ደግሞ ከኢህአዴግ ጐን በአጋርነት ተሠልፎ ይመራ የነበረው የወቅቱ አስተዳደር ይደግፍ ነበር፡፡ የክልሉ አመራሮች ስድስት ወር ህዝቡን ቤተመንግሥት ሆነው ይመራሉ፤ ስድስት ወር ይዋጋሉ፡፡ የኢፌዲሪ የመከላከያ ሠራዊትም በጦርነት ይማርክ የነበረው ዋናዎቹን ተዋጊዎች አልነበረም፡፡ እነሡ ቀን ተዋግተው ማታ ከከተማው ነዋሪ ጋር ተመሣስለው ይኖሩ ነበር፡፡ ሌላው ለኦብነግ የማታ ማታ መጠናከር አስተዋፅኦ ያበረከተው “ጅሃዲስት” ነኝ የሚለው አስተሣሠቡ ነው፡፡ ለማህበረሠቡ የሃይማኖት አባቶችና ሼካዎች “ከክርስቲያን መንግስት ጋር ነው የምዋጋው” እያለ ድጋፍ እንዲያደርጉለት ይጠይቃል፡፡

በዚህም ህዝቡ በየአመቱ በዘካ መልክ ገንዘብ እንዲሠጥ ተገደደ፣ የክልሉን በጀት የሚቆጣጠሩት እነሡ በመሆናቸውም የኢኮኖሚ አቅማቸው ፈረጠመ፡፡ ከተለያዩ የአረብ መንግስታት ጋርም ግንኙነት ፈጠረ፡፡ ከምዕራባውያን ጋር ሲገናኝም “ናሽናሊስት” (ብሄርተኛ) ነኝ ብሎ እርዳታ ይቀበላል፡፡ የገንዘብ ድጋፍ ሲያደርጉለት ከነበሩት ውስጥ የቀድሞው የሊቢያው መሪ መሃመድ ጋዳፊ በዋናነት ይጠቅሳሉ፡፡ ጋዳፊ በሡማሌ ክልል ለሚንቀሣቀሡ ታጣቂ ሃይሎች ከ5 ሚሊዮን ዶላር በላይ ድጋፍ ሠጥተዋል፡፡ ኳታርና ግብፅም ከፍተኛ ድጋፍ ያደርጉ ነበር፡፡ የውጭ ሃገር መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችም በተረጂዎች ስም እስከ 1999 ዓ.ም ድረስ ያመጡትን እርዳታ ለኦብነግ ያስረክቡ ነበር፡፡ ይህን ሁሉ ሚስጥር የፌደራል መንግስት አመራሮች አብጠርጥረው የተረዱት በ1999 ዓ.ም ነው፡፡ በወቅቱም የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ፣ በጉዳዩ ላይ ሠፋ ያለ ትንታኔ ያለው ፅሁፍ አዘጋጅተው እንደነበር አቶ አብዲ ይናገራሉ፡፡ በወቅቱ በተደረገው የተሃድሶ ጉባኤም የማጥራት እርምጃዎች ተወስደው በርካታ በሁለት ቢላዋ የሚበሉ አባላትና አመራሮች እንዲወገዱ ተደረገ፡፡ የፌዴራል መንግስት አስቀድሞ ችግሩን ባለመረዳቱ፣ ይህ ሁሉ የክልሉ የውስጥ ትግል ሲካሄድ ብዙም ድጋፍ አላደረገም ነበር፡፡

በ1999 ዓ.ም ግን አቶ መለስ ራሣቸው ዋነኛ ተሣታፊ በመሆን፣ የክልሉ ቀደምት ችግሮችን በመፍታት ትልቁን ድርሻ መወጣታቸውን አቶ አብዲ ገልፀዋል፡፡ በአሁን ወቅት ክልሉን የኢትዮጵያ ሶማሌ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢሶዴፓ) እየመራው ሲሆን ፕሬዚዳንቱም አቶ አብዲ መሃመድ ናቸው፡፡ ከሐምሌ 11 ቀን 2004 ዓ.ም ጀምሮም ቀደም ሲል “የሶማሌ ክልላዊ መንግስት” የሚለው ስያሜ በአዲስ መልክ “የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልላዊ መንግስት” ወደሚል ተቀይሮ በዚሁ ስያሜ እየተጠራ ይገኛል፡፡ ሌሎች የክልሉ አስተዳደር ቢሮዎችም “የኢትዮጵያ ሶማሌ” በሚል መነሻ ስያሜ እንዲጠሩ ተደርጓል፡፡ ክልሉ በመጪው ዓመት ህዳር 29 ቀን 2006 ዓ.ም 8ኛውን የብሄር ብሄረሠቦች በአል ለማዘጋጀት መመረጡ የሚታወስ ነው፡፡ የዚህ በአል አከባበር አካል የሆነው የመጀመሪያው የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት “የምስራቅ ኢትዮጵያን እንወቅ” በሚል መሪ ቃል ባለፈው ሰሞን የኪነጥበብ ባለሙያዎችና የሚዲያ ሠዎች እንዲሁም ፖለቲከኞች ወደ ክልሉ የተጓዙ ሲሆን አንፃራዊ ሠላም የሠፈነበት ክልሉ በአሉን ለየት ባለ መልኩ ለማክበር እየተዘጋጀ መሆኑን ለመረዳት ችለናል፡፡

Published in ህብረተሰብ

      በአሜሪካ ኮሎራዶ ግዛት የሚገኘው የአውሮራ የህዝብ ቤተመፅሃፍት ከ80 ዓመት በላይ ያስቆጠረ የዕድሜ ባለፀጋ ነው፡፡ የዕድሜ ብቻ ግን አይደለም፡፡ በመፅሃፍት፣በመረጃ፣በንባብና በዘመናዊ የቤተመፅሃፍት አገልግሎት አሰጣጥም የተደራጀና የበለፀገ ነው፡፡ ከሁሉም የሚገርመው ደግሞ ጅማሬው ነው- አነሳሱ፡፡ ይሄን የህዝብ ቤተመፅሃፍት የማቋቋም ሃሳብ የፀነሱት እ.ኤ.አ በ1925 ዓ.ም የከተማዋን ማደግ ተከትሎ የተመሰረተው የአውሮራ ሴቶች ክበብ አባላት ናቸው፡፡ እነዚህ ትጉህና በአዳዲስ ሃሳቦች የተሞሉ የክበቡ አባላት ከተማዋ እየሰፋች ፤የነዋሪዋ ቁጥር እየጨመረ ሲመጣ ለአዋቂዎችም ሆነ ለታዳጊ ህፃናት አገልግሎት የሚሰጥ የህዝብ ቤተመጽሃፍት እንደሚያስፈልጋት ያሰቡት ቀደም ብለው ነበር፡፡ ከሃሳብ በቀር ግን ቤሳቤስቲን አልነበራቸውም፡፡

የሁሉም ትላልቅ ፈጠራዎች መነሻ ሃሳብ (ህልም) ነው እንዲሉ… ሃሳባቸውን በወረቀት ላይ አስፍረው፤ዕቅድ ነድፈውና ግብ አስቀምጠው ወደተግባራዊ እንቅስቃሴ ገቡ፡፡ ቤተመፅሃፍት የማቋቋም ህልማቸውንም እውን ለማድረግ በቁርጠኝነት መትጋት ነበረባቸው፡፡ ገቢ ለማሰባሰብ ፓርቲ አዘጋጅተዋል፤ ሻይና ደረቅ ምግቦች ሸጠዋል፡፡ የፅህፈት መሳሪያዎችን ቸርችረዋል፡፡ ትያትር አዘጋጅተው አሳይተዋል-ለአዋቂዎች 25 ሳንቲም፤ ለህፃናት 15 ሳነቱም እያስከፈሉ፡፡ የአውሮራ ሴቶች ክበብ ለአራት ዓመት ባደረገው ከፍተኛ ጥረት ፌብሯሪ 10 ቀን 1929 ዓ.ም ሳራ የተባለች የክበቡ አባል በፈቀደችው አንዲት ክፍል ውስጥ ቤተመፅሃፍቱ ተከፈተ፡፡ የክበቡ አባላት ቤተመፅሃፍቱን ሲከፍቱ በእጃቸው ላይ የነበራቸው ገንዘብ 171ዶላር ብቻ ነበር፡፡ በአንዲት ክፍል ፤በአንድ የቤተመፅሃፍት ባለሙያና በ171 ዶላር ለከተማዋ የመጀመሪያ የሆነው ቤተመፃህፍት አገልግሎት መስጠት ጀመረ፡፡

ከአንድ ዓመት በኋላ በ1930 ዓ.ም የካፒታላቸው መጠን 200 ዶላር የደረሰ ሲሆን 3100 መፃህፍትና አንድ የቤተመፃህፍት ጠረጴዛ ነበራቸው፡፡ በዚህ ወቅት በዚህች አንድ ክፍል ውስጥ በአንድ ወር ብቻ 906 ተጠቃሚዎች መስተናገዳቸው ተመዝግቧል - በዚህችው አንዲት የቤተመፅሃፍት ባለሙያ፡፡ ከ20ዓመት በኋላ ቤተመፅሃፍቱ እያደገና እየሰፋ የመጣ ሲሆን ከተለመደው የቤተመፅሃፍት አገልግሎት በተጨማሪ አዳዲስ ዝግጅቶችም ተጀምረው ነበር፡፡ ለምሳሌ ታላላቅ የመፃህፍት ውይይቶች ከመደረጋቸውም ባሻገር፣ የበጋ የንባብ ፕሮግራም እና የህፃናት የትረካ ሰዓት የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ፡፡ በዚህ ሁሉ መሃል የክለቡ አባላት ከግለሰቦች እንዲሁም ቤት ለቤት እየዞሩ የመፅሃፍት ልገሳ የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ፡፡ አውሮራ ቤተመፅሃፍት አሁን ከተቋቋመ 84ኛ ዓመቱን ይዟል፡፡

በአንዲት ክፍል ቤት ተጀምሮ አራት ቅርንጫፎችን መክፈት ችሏል- ያውም ማራኪና ዘመናዊ በሆኑ ህንፃዎች ውስጥ፡፡ በ175 ዶላር የተጀመረው ቤተመፅሃፍቱ፤ እ.ኤ.አ በ2004 ዓ.ም ዓመታዊ በጀቱ 5ሚ. ዶላር ሊደርስ ችሏል፡፡ የሰራተኞቹ ቁጥርም 118 ደግሞ 118 ደርሷል፡፡ ይሄ ግን የበጎ ፈቃድ አገልጋዮችን አይጨምርም፡፡ በነገራችን ላይ አውሮራ ቤተመፅሃፍት ለህፃናት የመዋያና የመጫወቻ ስፍራዎችን ያዘጋጃል፤ ህፃናት በነፃ የስልክ አገልግሎት ትረካ የሚሰሙበት አሰራር ዘርግቷል፡፡ አረጋዊያንንም ግን አልዘነጋቸውም፡፡ የአዛውንት መጠለያ ማዕከላት ድረስ አገልግሎቱን ይሰጣል፡፡ ቤተመፅሃፍቱ ከመፅሃፍት፣ መፅሄቶችና ጋዜጦች በተጨማሪ የኢንተርኔትም አገልግሎት አለው፡፡ የኦንላይን መፃህፍት እንዲሁም ዲቪዲና ሲዲዎችም ያቀርባል፡፡ ይሄ ሁሉ እንግዲህ ከ80 ዓመት በፊት የተፀነሰ ታላቅ ሃሳብና ህልም ፍሬ ነው፡፡

Published in ባህል

                የዛሬውን ፖለቲካዊ ወግ የምጀምረው ባለፈው ሳምንት እዚሁ ጋዜጣ ላይ በወጣ አንድ አሳዛኝ ዜና ነው፡፡ እውነቱን ልንገራችሁ አይደል----እንደው ዝም ብለን እንፍጨረጨራለን እንጂ ገና ብዙ እኮ ነው የሚቀረን፡፡ (በሁሉም ነገር!) ከዚህ ቀደም አዲስ አበባ የአፍሪካ መዲና ሆና እንዴት የቆሻሻ ክምር ትሆናለች እያልን ዘራፍ እንል አልነበር? (ጉራ ብቻ ሆንን እኮ!) ባይገርማችሁ --- አሁን ነገርዬው ከዚያም ብሷል፡፡ እስቲ አስቡት--- በዘጠኝ ወራት ውስጥ ብቻ 22 ሰዎች ተቆፍረው በግዴለሽነት በተተዉ ጉድጓድ ውስጥ ገብተው ህይወታቸው አልፏል ይላል - አሳዛኙ ዜና፡፡

ማነው ለእዚህ ተጠያቂው ካላችሁ ደግሞ ---“ጀብደኞቹ” እነመብራት ሃይል፣ እነቴሌኮም፣ እነውሃና ፍሳሽ፣ እነመንገድ ትራንስፖርት እና እነ አካባቢ ጥበቃ መ/ቤቶች ናቸው ይላል - ዜናው፡፡ ቆይ ግን--- እቺ ከተማ ባለቤት የላትም እንዴ ? (የሚያስብላት አባት ወይም እናት ማለቴ እኮ ነው!) እሺ-- ወላጆቿ እንደሞቱባት ይታወቃል (አፄ ምኒልክና እቴጌ ጣይቱን ማለቴ ነው!) ግን እንጀራ እናት እንኳን የላትም እንዴ? አያት ቅድመአያትስ? በቃ--- ምንም ዘመድ የላትም ማለት ነው፡፡ (ባይኖራትማ! ነው) --- ሁሉም እየተነሳ እኮ ደህናውን መንገድ ቆፋፍሮ እብስ ነው የሚለው! ዘመድ ቢኖራትማ… 22 ነዋሪዎቿ የመንግስት መ/ቤቶች በቆፈሩት ቆፍረው በተውት ጉድጓድ ውስጥ እየገቡ ሲሞቱ የሚቆረቆርላቸው፣ ለቤተሰቦቻቸው የህይወት ካሳ እንዲከፈል ጥብቅና የሚቆም አይጠፋም ነበር፡፡

የአዲስ አበባ እሳትና ድንገተኛ አደጋዎች ኮሙኒኬሽን ኦፊሰር ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፣ ለደረሰው የህይወት ህልፈት ተጠያቂዎቹ ከላይ የተጠቀሱት የመንግስት ተቋማት ናቸው፡፡ እሳቸው “ተጠያቂ” ይበሏቸው እንጂ እስከዛሬ ግን የጠየቃቸው የለም፡፡ (“ሚስትህ ወለደች ወይ?” ቢሉት “ማንን ወንድ ብላ” አለ አሉ!) እውነቱን ለመናገር---ለዚህ ደግሞ ተጠያቂው አውራው ፓርቲያችን ኢህአዴግ ነው፡፡ በስልጣን ላይ በቆየባቸው ብቻ ሳይሆን በከረመባቸው 22 ዓመታት እቺን “ተጠያቂነት” የምትል ቃል ከዲስኩር ማሳመርያነት ባሻገር መሬት ላይ አውርዶ “ሊጠቀምባት” ወይም “ሊጠቅምባት” አልደፈረም፡፡

እንኳንስ እኛ ህዝቦቹ ይቅርና ራሳቸውም ተጠያቂዎቹ እኮ “ተጠያቂነት”ን በቅጡ አያውቁትም፡፡ (ተጠይቀው አያውቁማ!) በሌላ አነጋገር “ተጠያቂነት” የወረቀት ላይ “ነብር” ነው ማለት እንችላለን - እንደ አብዛኞቹ የጦቢያችን ህጐች! እናም መዲናችን ተጠያቂም ጠያቂም አጥታ ከምትባጅ ለምን መላ አንዘይድም፡፡ እንዴት ያለ አትሉኝም --- ለዚህች ባለቤት ላጣች ምስኪኗ መዲናችን “ሞግዚት” ብናፈልግላትስ? (ያውም የፈረንጅ ሞግዚት ነዋ!) ገንዘባችንን ይጭነቀው እንጂ ሞግዚት እኮ ሞልቷል - ከአውሮፓ አሊያም ከእስያ ማስመጣት እንችላለን፡፡ አያችሁ … ከተማ በማስተዳደር ጥሩ ልምድ ያለው የማኔጅመንት ተቋም (ዘመናዊ ሞግዚት ማለት እኮ ነው!) አስመጥተን መዲናዋን ይመራልናል (አገር በቀሎቹ አልሆንላችሁ ሲለንስ!) አይዟችሁ … የቅኝ ግዛት ነገር እንደሆነ አያሰጋንም፡፡ (በ21ኛው ክ/ዘመን ላይ እኮ ነን!) ደሞ ይሄ ሙያዊ እንጂ የኢህአዴግ ዓይነቱ የፖለቲካ ሹመት እኮ አይደለም! በዚያ ላይ የውጭውን ማኔጅመንት የምንፈልገው ለጥቂት ጊዜ ነው፡፡ ጥርስ ማውጣት ጀምሯል የተባለው ፓርላማችን፤ መንጋጋ እስኪያወጣ ብቻ! አያችሁ --- ፓርላማው መንጋጋ ያወጣ ዕለት “ተጠያቂነትም” የወረቀት ላይ ነብር መሆኑ ያከትምና የዱር ነብር ይሆናል!! ያኔ አዲስ አበባችንን ራሳችን ልናስተዳድር እንችላለን፡፡

(የተጠያቂነት ነብር አለና!) እኔ የምላችሁ … በቅርቡ በሰማያዊ ፓርቲ የተካሄደውን አወዛጋቢ የተቃውሞ ሰልፍ በተመለከተ አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ፤ “የኢህአዴግ ድራማ ነው!” ያሉት ነገር ገብቷችኋል እንዴ? ድራማው ምን እንደሆነ ስላልገባኝ እኮ ነው፡፡ የድራማ ነገር ከተነሳስ የሰሞኑ የኢህአዴግ ድራማ በጣም ተመችቶኛል --- አንዳንዴ ኢህአዴግ እያበዛው ነው እንጂ ፖለቲካ ሲባል እኮ ድራማ ነው፡፡ የእኛ አገር ብቻ ሳይሆን የዓለም ፖለቲካም ጭምር ድራማ ነው- የቀለጠ ትያትር! በነገራችሁ ላይ ባለፈው ማክሰኞ ማታ ከቤንሻንጉል ተፈናቅለው የነበሩ “የአማራ ተወላጆች” (አንዳንዶች “የኢህአዴግ ተወላጆች” ይሏቸዋል! ያደረጉትን የተቃውሞ ሰልፍ አያችሁልኝ … በአካል ሳይሆን በኢቴቪ! ከሰልፈኞቹ አንዷ ስለ ሰማያዊ ፓርቲ ምን ነበር ያለችው? “እነሱ ህገመንግስቱን ለማፍረስ የተነሱ ናቸው … ድብቅ የፖለቲካ አጀንዳቸውን ሊያራምዱ ፈልገው እንጂ ለእኛ አስበው አይደለም…” ወዘተ … ስትል የሰማኋት መሰለኝ (ኢተዓማኒ ድማራ ይሏችኋል ይሄ ነው!) አሁን እቺ ተፈናቃይ ሰልፈኛ ነች ወይስ ካድሬ? እንዴ … የሰልፉ ዕለት ማታ በኢቴቪ መግለጫ የሰጡት ሚኒስትር ዲኤታውም እንኳ እንደሷ አልተናገሩም እኮ! ይኸውላችሁ … አንዳንዴ ኢህአዴግ የድራማ ተዋናይ አመራረጥ ላይ ቀሽም ነው - “ካስቲንግ” አይችልበትም፡፡ አያችሁ … ተዋናይዋ እንደ ተፈናቀለ የአማራ ክልል ተወላጅ ሳይሆን ቅልጥ ያለች የኢህአዴግ ፖለቲከኛ ሆና ነው የተወነችው፡፡

(የአካባቢው ካድሬዎች ሂሳቸውን መዋጥ አለባቸው!) ምናልባት እኮ እሷ የተወነችው ህልሟን ሊሆን ይችላል። ኢህአዴግ ደግሞ የሷ ፖለቲከኛ የመሆን ህልም አይደለም ጉዳዩ -የሰማያዊ ፓርቲ አጀንዳ እንጂ። ለነገሩ … ህዝብን ሆኖ መተወን እኮ ከባድ ነው! (ህዝብን ይሆኑታል እንጂ አይመስሉትም!) የኢህአዴግ ካድሬዎች ግን ይሄን “ረቂቅ ጥበብ” የተረዱት አልመሰለኝም፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን በኢህአዴግ እርምጃ ተደስቻለሁ! (እሾህን በእሾህ የሚሉት ዓይነት እኮ ነው!) የሰማያዊ ፓርቲን ሰልፍ በኢህአዴግ ሰልፍ ነው የመከተው! (ያልተመጣጠነ እርምጃ ነው የወሰድኩት ብሎ ከመፀፀት ተርፏል!) አንዳንደ የታክሲ ረዳቶች (ወያላዎች) አንድን ሰው እንዲሳፈርላቸው ተለማምጠውት እምቢ ሲላቸው ምን እንደሚሉት ታውቃላችሁ? (ለነገሩ እናንተም ደርሶባችሁ ሊሆን ይችላል!) “ባቡሩ ሲመጣ ይወስድሃል” ይሉና ይፈተለካሉ (ከአፀፋ ምላሽ ሽሽት እኮ ነው!) ባቡሩ ምን እንደሆነ ገብታችኋል አይደል? መንገዱን ሁሉ እስርስር ያደረገብን የባቡር ሃዲድ ግንባታ ሲጠናቀቅ የሚመጣውን የከተማ ባቡር ማለታቸው እኮ ነው፡፡ እናንተ … የአራት ኪሎው ፓርላማ እኮ ፈፅሞ አልተቻለም፡፡ ከቀን ወደቀን ጡንቻ እያወጣ ነው።

የምክር ቤቱ አባላት “ጥርስ አውጥታችኋል” ሲባሉ “አናምንም፤ ድሮም ጥርስ ነበረን” አሉ እንጂ ትልቅ አብዮት እኮ ነው ያስነሱት! (ቀላል ቀወጡት!) እናላችሁ … ባለፈው ረቡዕ ማታ በኢቴቪ የቱሪዝምና ባህል ሚ/ርን ሲያፋጥጡ ደርሼ ምን ብሰማ ጥሩ ነው? የሉሲ የአሜሪካ ቆይታ በግልፅ ተብራርቶ ይነገረን ብለው ማፋጠጥ ያዙላችሁ! (ትርፍና ኪሳራዋን ማለታቸው መሰለኝ!) ሚኒስትሩም ሲመልሱ፤ ሁሉንም ገምግመን ስናጠናቅቅ ጥንካሬውንም ሆነ ከድክመታችን የተማርነውን ይሄ ነው ብለን እናቀርባለን” (ቃል በቃል ሳይሆን በደምሳሳው!) ምን ገረመኝ መሰላችሁ --- ፓርላማው ጡንቻ ማውጣት ከጀመረ አንስቶ “ከስህተታችን ተምረናል…”፣ “የአቅም ማነስ እንዳለብን ግንዛቤ ወስደናል”፣ “የአፈፃፀም ችግር እንዳለ ተማምነናል” ወዘተ … የሚሉ የመንግስት ሹመኞች በሽ በሽ ሆነዋል፡፡ እዚህች ጋ ግን አንድ ሃሳብ አለኝ … እኛን እየመሩ ከስህተታቸው ከሚማሩ ለምን ስልጣናቸውን አስረክበው ወደ ት/ቤት አይገቡም? ከምሬ እኮ ነው … እኛ ላይ ስህተት እየሰሩ መማርማ ከሰብዓዊ መብቶች ጥሰት የሚለይ አይደለም፡፡

ይሄውላችሁ … ወደ ት/ቤት መመለስ እኮ ሞት አይደለም - ይቻላል! ካላመናችሁኝ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ የነበሩትን እነ አቶ ልደቱና አቶ ስዬ፤ እንዲሁም ወ/ት ብርቱካንን ጠይቋቸው። ከስልጣን ወርደው አይደለም እንዴ በአሜሪካና በእንግሊዝ ዩኒቨርስቲዎች ትምህርት የጀመሩት። ይሄን ያደረጉት እኮ ለጉራ ወይም ለቅንጦት አይደለም፡፡ ህዝብ ላይ ስህተት እየሰሩ መማር ተገቢ አለመሆኑን ስለተረዱ ይመስለኛል። መንግስትም ቢሆን እኮ አባላቱ የከፋ ወንጀል እስኪሰሩ ጠብቆ ወህኒ ከመወርወር ይልቅ ገና ምልክቱ ሲታይባቸው ወደውጭ አገር ልኮ ቢያስተምራቸው ተመራጭ ነው - ጥቂት አባላቱንም ከነአካቴው ከመጥፋት ያተርፍ ነበር፡፡ (ከሰማኝ አይደል?) እኔ የምላችሁ ግን … ግብፆች ሳንወድ በግድ ድምፁን አጥፍቶ የተቀመጠውን አገራዊ ወኔያችንን ቀሰቀሱት አይደል? (ሳይቸግር ጤፍ ብድር አለ አበሻ!) እንግዲህ ከየመረጃ ምንጮቹ እንደሰማነው፤ የግብፅ መንግስትና ፖለቲከኞች የተስማሙት “ኢትዮጵያ የግድቡን ግንባታ እንድታቆም ማናቸውንም አማራጮች እንጠቀማለን” በሚል ነው፡፡

እኛ ጀግኖቹ የጦቢያ ልጆችስ? “ግድቡን ከመገንባት የሚያስቆመን የለም!” ( (ፈጣሪ የሰጠን ፀጋ እኮ ነው!) ለእስከዛሬውም ዓይን ዓይኑን ስናየው በመክረማችን በሰማይ ቤት ከመጠየቅ የምንድን አይመስለኝም! (አባይ እየተገማሸረ እኮ ነው ፆም ያደርነው!) ቆይ ቆይ … ግብፅ ምንድነው አለች የተባለው?” “የአባይ ተፈጥሯዊና ታሪካዊ ባለቤት እኔ ነኝ!” ምናምን ብላለች አይደል? ለካስ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ (ነፍሳቸውን ይማረውና) በዚያ ግብፃዊ ጋዜጠኛ ኢንተርቪው ሲደረግላቸው “በ21ኛው ክ/ዘመን እንዲህ ያለ አስተሳሰብ---” ያሉት ወደው አይደለም - ብሽቅ አድርጓቸው ነው! እስቲ አስቡት---አባይ ከአገራችን ጉያ እየሸለለና እያፏጨ ሲወጣ እያየነው---ጫፉን መንካት አትችሉም ስንባል! (የልጅ ጨዋታ አደረጉት እኮ!) እኔ ግን ያልገባኝ ምን መሰላችሁ---- ግብፅ ግድቡን እንዳንገነባ የፈለገችው ውሃው ይቀንስብኛል ብላ ሰግታ ነው ወይስ በደረቅ ምቀኝነትና ንቀት ተገፋፍታ ምክንያቷ የትኛውም ቢሆን ግን “አንተ አብራ፤ እኔ ልብላ!” እንደማለት ነው፡፡ ወይም “ከባልሽ ባሌ ይበልጣል” እንዳለችው ራስ ወዳድ ሚስት መሆኗ ነው፡፡ ይሄ ደግሞ አያዋጣም - (ኧረ ስንዝር አያስኬድም!) እኛ ግን “ጦርነት የታከተን ህዝቦች ስለሆነን ምርጫችን አናደርገውም” (ካልተገደድን በቀር!)

ኢትዮጵያ የት እንዳለች የማያውቁ የአፍሪካ ጋዜጠኞች ገጥመውኛል... የሰው ዘር መገኛ ኢትዮጵያ ናት ኬንያ?

በቅርቡ ለጋዜጠኞች በተዘጋጀ ስልጠና ለመካፈል ወደ ናይሮቢ ኬንያ ተጉዤ ነበር፡፡ በእርግጥ የመጀመሪያዬ አልነበረም፡፡ ግን ይህኛው ለየት ያለ ነገር ነበረው፡፡ አጋጣሚው ከአርባ አምስት የአፍሪካ ሃገራት የመጡ በርካታ ጋዜጠኞችን አሰባስቧል፡፡ ሁሉም ስለ ሃገሩ ይናገራል፣ ስለሌላውም ይጠይቃል፡፡ እኔም እንዲሁ ከሚጠይቁትና ሃገራቸውን ከሚያስተዋውቁት መካከል አንዱ ሆንኩኝ፡፡ ምናልባት ወደ ሃምሳ ጋዜጠኞች ይሆናሉ የተጋበዙት፡፡ ከኢትዮጵያ እኔ ብቻ ነበርኩ፡፡ በተለያዩ ጊዜያት ሞቅ ያለ ውይይትና ትውውቅ እናደርጋለን፣ ሃሳብ እንለዋወጣለን፡፡ አብዛኞቹ ስለ ኢትዮጵያ ለማወቅ የነበራቸው ጉጉት ገርሞኛል፡፡

እኔ ኢትዮጵያን በሚገባ ያውቋታል ብዬ ሳስብ በተቃራኒው ምንም ዓይነት መረጃ የሌላቸው ሰዎች አጋጥመውኛል፡፡ በዚህ ቆይታዬ ጋዜጠኞቹ ስለ ኢትዮጵያ ያላቸው ግንዛቤ ምን እንደሚመስል መረዳት ችያለሁ፡፡ በዚህች አጭር ፅሁፌ ከጋዜጠኞቹ የታዘብኩትን ላጋራችሁ እወዳለሁ፡፡ በናይሮቢ ያሰባሰበን ድርጅት ፓን-አፍሪክ በሚባል ጉደኛ ሆቴል የእራት ግብዣ አደረገልን። የመዝናኛ ፕሮግራምም ነበረው፡፡ የመድረክ መሪው ኬንያን ለማስተዋወቅ ይጠቀምበት የነበረው መንገድ በጣም ይገርማል፡፡ አፍሪካ ያለ ኬንያ ምንም አይደለችም የሚያስብል ነበር፡፡ ‹‹የሰው ዘር መገኛ ወደ ሆነችው ኬንያ እንኳን በሰላም መጣችሁ›› ብሎ ጀመረ፡፡

‹‹ዓለም በዚህ ብቻ አይደለም የሚያውቀን። ውብ የሆነው የእንግዳ ተቀባይነት አፍሪካዊ ባህልም መፈጠሪያው እዚህ ነው፡፡ እርግጠኛ ነኝ ወደየሃገራችሁ ስትመለሱ ለዓለም ህዝብ ስለዚህ ውብ ኬንያዊ ባህል እንደምትመሰክሩ…….››እያለ ቀጠለ፡፡ ወይ ጉድ አልኩኝ በውስጤ፡፡ በተለይ የሰው ዘር መገኛ የሚለው አባባሉ በጣም ከነከነኝ፡፡ ይህ የታሪክ ሽሚያ ነው ወይስ የሳይንሳዊ መረጃ መፋለስ። ይህን አባባል እኛ በሰፊው እንጠቀምበታለን፣ ኬንያውያንም እንዲሁ፡፡ ዓለም ማንኛችንን ይመን? በዚህ ሆቴል እራት እየበላን ነው፡፡ ከፊት ለፊቴ ማላዊትዋ ሰሊና ተቀምጣለች፡፡ ስለ ኢትዮጵያ የምታውቀውን ትናገራለች፡፡ እኔን ጨምሮ ብዙ ጋዜጠኞች እንሰማታለን፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ በራስታዎች ትታወቃለች፡፡ በጃማይካና በሌላውም ዓለም የሚገኙ ራስታዎች የህይወት ዘመን ምኞታቸው ኢትዮጵያ ውስጥ ሄደው መኖር ነው፡፡ በራስ ተፈሪ ያመልካሉ፣ ነብያችን ናቸው ይሉዋቸዋል፡፡ በነገራችን ላይ አፄ ሃይለስላሴ በማላዊ በጣም ይታወቃሉ፡፡

ዋናው መንገዳችን በሳቸው ነው የተሰየመው፡፡ ኮረብታ ላይ የተገነባ አንድ በጣም ጥንታዊና የሚያምር ሆቴልም በሳቸው ስም ይጠራል›› አለችን፡፡ ይህኛው ታሪክ በጣም ተመቸኝ፣ ከዛም አልፎ ሲበዛ አስደነቀኝ። በሃገራቸው አንድም ማስታወሻ የሌላቸው ንጉስ በሰው ሃገር ብዙ ይባልላቸዋል፡፡ እኔም በተራዬ አንድ ጥያቄ ሰነዘርኩላት ‹‹ባለፈው ዓመት የተሾመችው ፕሬዚዳንታችሁ እንዴት እየሰራች ነው፣ እስቲ ስለሷ ንገሪኝ? በሐምሌ 2004 ዓ.ም ማላዊ መካሄድ የነበረበት የአፍሪካ ህብረት ስብሰባ በሃገሬ አይካሄድም በማለቷ በአዲስ አበባ ተደረገ፡፡ ይህ የሆነው የሱዳኑን ፕሬዚደንት አልበሽርን ለዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት አሳልፌ ነው የምሰጠው በማለቷ ነበር፡፡

እሷ ግን ለአፍሪካ ህብረት ህገ ደንብ አትገዛም ማለት ነው?›› አልኳት። ሰሊና ስትመልስም ‹‹ምን መሰለህ አንደኛ ነገር ባለቤቷ የፍትህ ሚኒስትር ነው፡፡ ስለዓለምዓቀፍ ህግ ጠንቅቆ ያውቃል፣ በዚህ ላይ ዋና አማካሪዋ ነው፡፡ ማላዊ ለዓለም አቀፉ ፍርድቤት ፈርማለች፣ ስለዚህ አልበሽር እዛ ቢገኝ አሳልፋ ነው የምትሰጠው፡፡ እዚህ አበሳ ውስጥ ከመግባት ግን ስብሰባው ማላዊ ውስጥ እንዳይካሄድ ማድረግ ተመራጭ ነበር፡፡ ሁለተኛ ለአፍሪካ ህብረት ህገ-ደንብ ተገዢ አትሆንም ወይ ላልከው ተገዢ መሆን የለባትም። የአፍሪካ ህብረት እኮ የአምባገነኖች ስብስብ ነው። አስበው እስቲ ኢትዮጵያ ውስጥ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ዜጎችን ያረደው መንግስቱ ሃይለማርያም እኮ ዚምባብዌ ውስጥ ነው የመሸገው፡፡

የአፍሪካ ህብረት ለአፍሪካ ህዝቦች ፍትህና ብልፅግና የቆመ ተቋም ቢሆን ኖሮ ሮበርት ሙጋቤን አሳምኖ መንግስቱን ለፍርድ ያቀርበው ነበር፡፡ ግን አላደረገውም፡፡ ስለዚህ አፍሪካ ህብረት ማለት ህዝባዊ ሃላፊነት የማይሰማቸው ሰዎች ተሰባስበው የገነቡት ተቋም ነው›› አለችኝ፡፡ እውነቷን ነው፣ በዚህ አባባሏ በከፊል እስማማለሁ፡፡ ከዚህ አንፃር ሲታይ አህጉራዊው ተቋም ብዙ የቤት ስራ እንደሚቀረው አምናለሁ፡፡ ታንዛኒያዊው ኪዜቶ የዛምቢያው አሮንን ስለ ኢትዮጵያ ያጫውተዋል፡፡

በመሃል ተቀላቀልኩዋቸው፡፡ አንድ ጥያቄ ጠየቀኝ ‹‹አሁን አንድ መፅሃፍ እያነበብኩ ነው፣ አርዕስቱ ‘ዘ አፍሪካን ስቴትስ’ ይላል፡፡ እዛ መፅሃፍ ላይ መንግስቱ ሃይለማርያም የ1977ቱን ድርቅ ለዓለም ህዝብ ለመንገር ፈቃደኛ እንዳልነበር አንብቤያለሁ። በጣም አዘንኩ፣ ለምን ግን መደበቅ ፈለገ?››፡፡ ጉዳዩ የፖለቲካ ጨዋታ እንደነበር መለስኩለት፡፡ ‹‹ለመንግስቱ ሃይለማርያም ፖለቲካው እንጂ የህዝቡ መራብ ጉዳዩ አልነበረም፡፡ በወቅቱ ኢትዮጵያ ተርባለች ብሎ ማወጅ ለእሱ ውርደት ነበር፣ እናም አይኑ እያየ ብዙ ህዝብ አለቀ፡፡ የአምባገነን መሪዎች አንዱ መገለጫ ይህ ነው፣ የሚኖሩት ለህዝቡ ሳይሆን ለራሳቸው ዝናና ክብር ነው›› አልኩት፡፡ የደቡብ አፍሪካዋ ካትሪን ቀጠለች ‹‹ያኔ እነ ቦብ ጌልዶፍ ባይደርሱላችሁ ኖሮ እርግጠኛ ነኝ ታልቁ ነበር፡፡

ጌልዶፍና ቦኖ ባዘጋጁት ኮንሰርት ብዙ እርዳታ አሰባስበዋል፣ ሚሊዮኖችን እንደታደጉም እገምታለሁ›› አለችኝ፡፡ እሷ ባለችው ተስማማሁ፡፡ያ የዕርዳታ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ያስከተለውንም መዘዝ እያሰብኩኝ፡፡ እውነቷን ነው፣ የጌልዶፍ የዕርዳታ ጥሪ 150 ሚሊዮን ፓወንድ በማሰባሰብ በርካቶችን ከሞት ታድጓል፡፡ ግን ደግሞ የታላቋን ሃገር ስምና ዝና ለዘላለም እንዳጎደፈው ማን በነገራት አልኩኝ በውስጤ፡፡ ዓለም ዛሬም ድረስ ኢትዮጵያን የሚያውቃት ይኸው ሰውዬ ባዘጋጀው ኮንሰርት ላይ በመላው ዓለም በቴሌቪዥን መስኮት በአራት መቶ ሚሊዮን ህዝብ ዘንድ በደረሱ የተራቡ ህፃናት ምስል ነው፡፡ ከያኔው ጀምሮ ኢትዮጵያና ረሃብ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታ ሆነው ይጠራሉ፡፡ ከ1958-1961 ዓ.ም ባጋጠመው በታላቁ የቻይና ረሃብ ወደ 43 ሚሊዮን የሚሆኑ ሰዎች ቢያልቁም የቻይና ስም ግን የኢትዮጵያን ያህል አልጎደፈም፡፡ አንዳንዴ ሳስበው ምነው በቀረብን እላለሁ፡፡

ውይይታችን ቀጠለ፣ ጨዋታውም ደርቷል። ሁሉም በየተራ ይናገራሉ፡፡ ሂልማ የናሚቢያ ጋዜጠኛ ነች፡፡ ሃገሯን ለማስተዋወቅ የነበራት ጉጉት የሚገርም ነበር፡፡ በደንብ ተዘጋጅታ መጥታለች። በሃገሯ የሚታተሙ ጋዜጦች፣ የተለያዩ ፅሁፎችና የናሚቢያ የቱሪስት መስህብ የሆኑ አካባቢዎችን የሚያስተዋውቁ ብሮሸሮች ሰጠችን፡፡ በፎቶና ቪድዮ የተደገፈ የማስተዋወቅ ስራ በማከናወን ሁላችንም ስለ ናሚቢያ የተወሰነ ግንዛቤ እንዲኖረን አድርጋለች፡፡ ሂልማን ስለ ኢትዮጵያ የምታውቀው ነገር ይኖር እንደሁ ጠየቅኳት፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ ምዕራብ አፍሪካ ውስጥ ነው የምትገኘው?›› በማለት ጥያቄዬን በጥያቄ መለሰችልኝ፡፡ የአፍሪካ መዲና የሆነችውን ሃገር እንዴት አታውቃትም ብዬ ራሴን ጠየቅሁ። ከዚህ በኋላ ማድረግ የነበረብኝ ነገር የቻልኩትን ያህል ስለ ኢትዮጵያ መንገር ነው፡፡

በዚህ ቆይታችን ጥሩ ግንዛቤ እንዳገኘች ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ከጎኔ የተቀመጠው ኡጋንዳዊ ጋዜጠኛ ፒተር በአዲስ አበባ ከጓደኞቹ ጋር ሲዝናኑ ስላጋጠማቸው ሁኔታ ሊነግረኝ ጓጉቷል፡፡ እስቲ ልስማው ብዬ ጆሮ ሰጠሁት፡፡ አብረውን የተቀመጡ ሰባት ጋዜጠኞች ነበሩ፡፡ ፒተር ቀጠለ ‹‹በአፍሪካ ህብረት ጉባኤ ለመሳተፍ ወደ አዲስ አበባ ሄደን ነበር፡፡ አልጋ የተያዘልን ሒልተን ሆቴል ነው፡፡ መሸትሸት ሲል ከሂልተን ሆቴል አራት ሆነን ለመዝናናት ወጣን፡፡ በሩ ጋ ስንደርስ የጎዳና ተዳዳሪዎች የሆኑ ህፃናት አገኘን፡፡ ከሌላ ሃገር እንደመጣን ወድያውኑ ለዩን፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ አንዱ ችግር ይሄ ነው፣ መመሳሰል አይቻልም፣ ማንም ሰው አይቶ ኢትዮጵያዊ እንዳልሆንክ በቀላሉ ይለይሃል፡፡ እነዚህ ህፃናት በዝቅተኛ ዋጋ የምንዝናናበት ቦታ ሊያሳዩን እንደሚፈልጉ ነገሩን፣ ተስማምተን ሄድን፡፡

የሆነ ጊቢ ውስጥ አስገቡን፣ መብራቱን አጠፉት፣ ከሁሉም አቅጣጫ ወሮበሎች ተሰባሰቡና የያዝነውን በሙሉ ዘርፈው አስወጡን፣ ይህን አጋጣሚ መቼም አልረሳዉም›› አለ፡፡በመሃል እኔ ቀጠልኩ ‹‹ኢትዮጵያ የነፃነት ሃገር ነች ስላችሁ ገነት ነች ማለት አይደለም፡፡ አልፎ አልፎ ችግር ያጋጥማል፡፡ በተለይ ደግሞ እንደ እናንተ ዓይነት እንዝላልነት ሲታከልበት ነገሩ የከፋ ይሆናል፡፡ሁሌም እንግዳ የሆነ ሰው የተወሰነ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለበት እገምታለሁ፡፡ እንዴት የማላውቀውን ሰው ተከትዬ ናይሮቢ ወዳሉት መዝናኛ ቤቶች እሄዳለሁ›› አልኩት፡፡ ሁሉም ተስማሙ፡፡ ፊሊፕ ኬንያዊ ነው፣ ከዚምባብያዊ ጓደኛው ማርኮ ጋር ይጫወታል፡፡ ስለ ኢትዮጵያውያን ቆነጃጅት አውርቶ የሚጠግብ አይመስለኝም፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ የቆነጃጅት ምድር ነች፣ እዚህ የምታያቸው ጋዜጠኞች ሁሉ አዲስ አበባን ቢያዩዋት ኖሮ ቤታቸውን እዛ ይገነቡ ነበር፡፡ ልንገራችሁ የዓለም ቆንጆ ያለው አዲስ አበባ ውስጥ ነው፡፡ Addis is a home of love. አዲስ አበባ የፍቅር ሃገር ነች፡፡ የአፍሪካ መዲና መሆኗ ይገባታል፡፡

ብዙ የሚያዝናኑ ነገሮች አሏት……›› እያለ ስለ ኢትዮጵያ በጎ ነገሮች መናገሩን ቀጠለ፡፡ እኔም ተቀብየው ቀጠልኩ፡፡‹‹ፊሊፕ እንዳለው ኢትዮጵያ የውበት መንደር ነች፣ የዓለም ቆነጃጅት መኖሪያም ጭምር፡፡ የዋህና እንግዳ አክባሪ፣ በታሪኩና በማንነቱ የሚኮራ፣ ለአፍሪካውያን ነፃነት፣ ደህንነትና ብልፅግና የሚተጋ ህዝብ አላት፡፡ አዲስ አበባ የፍቅር፣ የህይወትና የነፃነት ከተማ ነች። Welcome to Addis Ababa: a City of Love, Life and Freedom ብዬ የጉብኝት ግብዣ አቀረብኩላቸው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ነፃነት በእጅጉ የሚያኮራ እንደሆነ አፌን ሞልቼ መናገር ችያለሁ፡፡ ሃገራችን ወንጀል እምብዛም ያልተበራከተባት ስለሆነች ከየትኛውም የዓለም ክፍል የመጡ እንግዶች በነፃነት ነው የሚንቀሳቀሱት፡፡ ኬንያዊቷ ጋዜጠኛ በአንድ ወቅት ስትነግረኝ ‹‹ናይሮቢ ውስጥ እየሄድክ ስልክ ቢደወልልህ በነፃነት ማውራት አትችልም፡፡ የሆነ ቦታ ተደብቀህ ነው የምታናግረው፡፡

አዲስ አበባ ግን በነፃነት የፈለከውን ያህል ታወራለህ፣ በማንኛውም ጊዜና ቦታ ምንም ያህል ብትዞር ወንጀል እስካልሰራህ ድረስ ሃይ ባይ የለህም፡፡ ለእኔ ነፃነት ማለት ይህ ነው››ብላኛለች፡፡ እውነቷን ነው፣ ናይሮቢ ውስጥ የውጭ ሃገር ዜጎች ያለ ፓስፖርት መንቀሳቀስ አይችሉም፡፡ ፖሊስ ያስቆማቸውና ይጠይቃቸዋል። ከሌላቸው የሆነ ጉራንጉር ውስጥ ወስዶ ያላቸውን ዘርፎ እስር ቤት ያስገባቸዋል፡፡ በዚህ ምክንያት በዚያች ሃገር የመንቀሳቀስ ነፃነት ያለ ህግ የተገደበ ነው፡፡ ኡጋንዳዊው ጌራልድ ስለ ኢትዮጵያ የተወሰነ እውቀት አለው፡፡ ‹‹የህዳሴው ግድብ ግንባታ እንዴት እየሄደ ነው?›› ብሎ ጠየቀኝ፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ተባብሮ ግንባታውን እያፋጠነው እንደሆነ ነገርኩት፡፡ ቀጠለ ጌራልድ ‹‹ግብፆቹ ደግሞ በጣም እየተንጫጩ ነው፡፡ ውሃውን ለብቻቸው እንዲጠቀሙበት ነው የሚፈልጉት›› አለኝ። ትክክል ብለሃል፣ ወንዙን ላለፉት በርካታ ዓመታት እንዳደረጉት ሁሉ ለብቻቸው ለመጠቀም ይፈልጋሉ፡፡ ለዛ ነው ነጋ ጠባ የሚንጫጩት። ኢትዮጵያ ግድቡን የምትገነባው እነሱንም ለመጥቀም ነው፡፡ ግድቡ ሲጠናቀቅ የሚመነጨው ሃይል ለነሱም ይደርሳል፡፡ ይህን ውሃ ለሃይል ማመንጫነት ነው የምንጠቀምበት፡፡ ውሃው ሃይል አመንጭቶ እንደተለመደው ወደ ግብፅ ይሄዳል። ስለዚህ ተቃውሟቸው ብልሃት ይጎድለዋል ብዬ ውስጤ የነበረውን ንዴት ጭምር ተነፈስኩለት፡፡

‹‹ኢትዮጵያ በመለስ ዜናዊ አመራር በጣም ተራምዳለች፣ ሁሌም ስለ ኢትዮጵያውያን የሚገርመኝ አንድ ነገር አለ፡፡ እንሰራለን ካሉ በአንድ ልብ ተነሳስተው ይሰራሉ፣ ለለውጥ ይነሳሉ። በእኛ ሃገር የሌለው ይህ ነው፡፡ ህዝቡ በጣም የተከፋፈለ ነው፣ አንድ ሆኖ አያውቅም፣ በዚህ መልኩ ኡጋንዳን ማሳደግ የምንችል አይመስለኝም›› አለ፡፡ ለጌራልድ ያለኝን አድናቆት ገልጬ ወደ ኬንያዊው ጋዜጠኛ ሄድኩኝ፡፡ ኬምቦይ ይባላል፡፡ በዚህ ጉዞዬ የታዘብኩት አንድ ነገር አለ፡፡ ኬንያውያኑ ችግር አለባቸው፡፡ አፍሪካ የምትባለዋን አህጉር እነሱ የሰሩዋት ነው የሚመስላቸው፡፡ ኬንያ የአፍሪካ እስትንፋስ ነች፣ ህዝቦቿ ደግሞ የአፍሪካዊ ማንነት መገለጫዎች ናቸው ይላሉ፡፡ ከነሱ በላይ አፍሪካዊ ላሳር ነው፡፡ ኬምቦይ በዚህ መንፈስ ነበር የተዋወቀኝ። ‹‹ወደ እውነተኛው የአፍሪካ ምድር እንኳን በደህና መጣህ›› አለኝ፡፡ የአፍሪካ የነፃነት ተምሳሌት ከሆነች ሃገር ለሄደ ሰው ይህ አባባል ትንሽ ይጎረብጣል፡፡ ለማንኛውም መልስ መስጠት ነበረብኝ።

I am from the heart of Africa, Ethiopia, nice to meet you. የአፍሪካ ማዕከል ከሆነችው ኢትዮጵያ ነው የመጣሁት፣ ስለተዋወቅን ደስተኛ ነኝ ብዬ መለስኩለት፡፡ ኬምቦይ ቀጠለ ‹‹ኢትዮጵያን አይቻት አላውቅም፣ ማየት አለብኝ። ከእንግዲህ ከምጎበኛቸው ሃገሮች ቀዳሚ የምትሆነው አዲስ አበባ ነች፡፡ ወዳጆች ነን፡፡ ጥሩ ግንኙነት አለን፣ ብዙ የምንጋራቸው ነገሮች አሉ፡፡ ግን አሁን አሁን ኢትዮጵያ ኬንያን ለመጉዳት እየሰራች ነው፣ ለምን እንደዛ ታደርጋላችሁ? የጊቤ ሶስት የሃይል ማመንጫ ግድብን በመስራታችሁ ልትኮሩ አይገባም፡፡ በታችኛው ተፋሰስ ያሉ ኬንያውያንን ይጎዳል፣ የቱርካና ሃይቅም ጨዋማ ይሆናል፣ የውሃ መጠኑ ይቀንሳል፡፡ ሌላው ደግሞ በኬንያ ድንበር የሚገኙ ጎሳዎቻችሁ የእኛን ዜጎች እያሰቃዩዋቸው ነው፡፡ ድንበር ጥሰው በመግባት ከብቶቻቸውን ይዘርፉባቸዋል›› አለኝ፡፡ የዚህን ጋዜጠኛ የተዛባ አመለካከት በተገቢው መንገድ ማስተካከል ነበረብኝ።

‹‹ግድቡ የታችኛው ተፋሰስ ህዝቦችን የሚጎዳ ከሆነ የሚጎዱት የእናንተ ዜጎች ብቻ አይደሉም፣ የእኛም ናቸው፡፡ ምክንያቱም ይህን ወንዝ ተከትለው የሚኖሩ የደቡብ ኦሞ ህዝቦች አሉን፡፡ እኛ ደግሞ ህዝባችንን ለመጥቀም እንጂ ለመጉዳት የምንሰራው ነገር የለም፡፡ እኛ በምንሰራው ስራ ዜጎቻችንን ጠቅመን ጎረቤቶቻችንም እንዲጠቀሙ ነው የምንፈልገው፡፡ አሁን ለጂቡቲና ለሱዳን የኤሌክትሪክ ሃይል መላክ ጀምረናል፣ ቀጥለን ለእናንተም እንልካለን፡፡ ስለዚህ እኛ በምንሰራው ስራ እናንተም ተጠቃሚዎች ናችሁ፡፡ አሁን አንተ የምትለኝ ቀደም ሲል “ፍሬንድስ ኦፍ ሌክ ቱርካና” የሚባል ድርጅት ያናፈሰው መሰረት የሌለው ወሬ ነው፡፡ የወንዙ ፍሰት በምንም መልኩ የሚቀንስ ወይም የሚቋረጥ አይደለም። የጎሳዎቹን ግጭት ለማርገብ ደግሞ ሁለቱም መንግስታት በጋራ እየሰሩ እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ የሁለቱም ሃገራት ግንኙነት ተጠናክሮ ይቀጥላል የሚል እምነት አለኝ›› በማለት ላስረዳው ሞከርኩ፡፡ ሆኖም ግን የተዋጠለት አይመስለኝም፡፡ በስልጠናው መሃል የውይይት ጊዜ ነበር። የምንወያየው በቡድን ተከፋፍለን ነው፡፡ እናም በሁለተኛው ቀን ሁላችንም በአምስቱም የአፍሪካ ቀጣና ተከፋፍለን እንድንወያይ ተፈለገ፡፡ የትኛው ሃገር በየትኛው ቀጠና እንደሚመደብ መነጋገር ተጀመረ፡፡ የምስራቅ አፍሪካ ሃገራት ዝርዝር መጥራት ሲጀመር ኢትዮጵያ የለችበትም፡፡ አንዱ እጁን አወጣና ‹‹ኢትዮጵያ ሰሜን አፍሪካ ውስጥ ነው የምትመደበው?›› ብሎ ጠየቀ፡፡ አስተባባሪው መልስ ሰጠ ‹‹ኢትዮጵያ ምስራቅ አፍሪካ ውስጥ ነው ያለችው፡፡ የሶማሊያ ጎረቤት ነች፡፡

ለዛ እኮ ነው ከአልሸባብ ጋር የምትዋጋው›› አለ፡፡ ከዚህ በኋላ እኔና ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ ቀጠና ውስጥ ተካተትን፡፡ ከዚህ ምደባ በኋላ ለእያንዳንዱ ቡድን አስተባባሪ እንዲመደብ ተፈለገ፡፡ አስተባባሪዎች በምን መንገድ ይመረጡ ሲባል ምርጫ ይካሄድ ተባለ፡፡ በዚህ ውሳኔ መሰረት ለምስራቅ አፍሪካ ጋዜጠኞች አስተባባሪ ለመምረጥ ዕጩዎችን የመጥራት ሂደት ተጀመረ፡፡ ከተለያዩ ሃገራት ሶስት እጩዎች ተጠሩ፡፡ ከኢትዮጵያ ግን ዕጩ የሚጠራ ሰው ጠፋ፡፡ በዚህ ጊዜ እጄን አውጥቼ ራሴን በእጩነት አቀረብኩ፡፡ አዳራሹ በሳቅ ታወከ፡፡ ሆኖም ተቀባይነት አግኝቼ እጩ ተወዳዳሪ ሆንኩኝ፡፡ ከእኔ ጋር አራት ዕጩዎች ቀረብን፡፡ ምርጫው ተጀመረ፣ የታንዛኒያው ኪዜቶ አብላጫውን ድምፅ ሲያገኝ ለእኔ ግን ድምፅ የሰጠሁት እኔ ብቻ ነበርኩ፡፡ በስልጠናው አዳራሽ ከሩዋንዳውጋዜጠኛ ፍሬድሪክ ጎን ነበር የተቀመጥኩት፡፡ ስለ ኢትዮጵያ መናገር ፈልጓል፡፡ ሩዋንዳውያን ስለ ኢትዮጵያ ጥሩ አመለካከት አላቸው፡፡

ያኔ እርስ በርሳቸው ሲጨፋጨፉ የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ ሃይል ደርሶላቸዋል፡፡ ይህን ታላቅ ተግባር ሁሌም ያስቡታል፡፡ የሃገሪቱ መሪ ፖል ካጋሜ በአቶ መለስ የቀብር ስነ ስርዓት ተገኝተው የተናገሩትን አስታውሳለሁ፡፡ ‹‹መለስና የኢትዮጵያ ህዝቦች በሃገራችን ከተፈፀመው አሰቃቂ እልቂት ማግስት ሰላም ለማስፈን ያደረጉትን ድጋፍ የሩዋንዳ ህዝቦች መቼም ቢሆን የሚዘነጉት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ ይህን ድጋፍ ያደረገችው ራሷ ገና በሽግግር ሂደት ላይ በነበረችበት ወቅት ነበር›› ብለዋል፡፡ ከፍሬድሪክ ጋር ወጋችንን ቀጠልን፡፡ “እስቲ ስሜን በአማርኛ ፊደል ፃፍልኝ” አለኝ፣ ፃፍኩለት። እሱም ደጋግሞ ሞከረው፡፡ ‹‹ኢትዮጵያውያን እጅግ ልትኮሩ ይገባችኋል፣ ከአፍሪካ ሃገራት ውስጥ የራሳችሁ የቀን አቆጣጠርና ፊደል ያላችሁ ብቸኛ ሃገር ናችሁ፡፡ ከአምስት ዓመት በፊት የራሳችሁን አዲስ ሚሌንየም ማክበራችሁን ሰምቻለሁ፡፡ የሰዓት አቆጣጠራችሁም እንዲሁ የተለየ ነው፡፡ በርግጥ ግራ እንደሚያጋባ አንድ ጓደኛዬ ነግሮኛል፡፡ አሁን በናንተ አቆጣጠር ስንት ሰዓት ነው?›› ብሎ ጠየቀኝ። ጥቂት ማብራሪያ ሰጥቼ ፍሬድሪክን ተለየሁት። ከኋላዬ የተቀመጠው ከቡሩንዲ የመጣው ሉሙምባ እንድተዋወቀው ይጎተጉተኛል፡፡ ወደሱ ዞርኩኝ፡፡ ከብዙ በጥቂቱ ስለ ኢትዮጵያ አየር መንገድ የነገረኝን ላጋራችሁ፡፡

‹‹አየር መንገዳችሁ በዓለም አሉ ከሚባሉት ውስጥ ይመደባል፣ ምቾቱ፣ መስተንግዶው፣ ደህንነቱ፣ ዘመናዊነቱ ልዩ ነው፣ አስተናጋጆቹም በጣም ያምራሉ፡፡ ግን አንድ ችግር አለው፣ በዓለም አቀፍ በረራ ሰዓት አያከብርም፣ የመንገደኞች ሻንጣም በተደጋጋሚ ይጠፋል›› በማለት ጥሩውንም መጥፎውንም ነገረኝ፡፡ ይህን ቅሬታ እንዳለ ዋጥኩት፣ ምክንያቱም አየር መንገዳችን በዚህ ነገር በተደጋጋሚ እንደሚወቀስ ከእሱ በላይ ጠንቅቄ አውቃለሁ፡፡ ከናይጄሪያዊው ጋዜጠኛ ጋር ለመተዋወቅ ወንበር ቀየርኩኝ፡፡ ‹‹አታዪ እባላለሁ ናይጄሪያዊ ነኝ›› ብሎ ተዋወቀኝ፡፡ ገ/ሚካኤል እባላለሁ ኢትዮጵያዊ ነኝ ብዬ ራሴን አስተዋወቅኩ፡፡ ‹‹ሚካኤል የክርስቲያኖች መልዓክ ነው፣ ክርስቲያን ነህ እንዴ?” አለኝ፤ አዎ አልኩት፡፡ “ይገርማል! ኢትዮጵያ ውስጥ ክርስቲያኖች አሉ ማለት ነው?›› ብሎ ቀጠለ፡፡ በዚህ ጥያቄው እኔን ሳይገርመኝ በእኔ መልስ እሱ መገረሙ ገረመኝ፡፡ እንዴት ስለ ኢትዮጵያ መረጃ የለውም፣ በውስጤ የሚመላለስ ጥያቄ ነበር፡፡ ያውም ከረዥም ጊዜ ጀምሮ የክርስቲያኖች ሃገር እየተባለች የምትጠራዋን ኢትዮጵያ፡፡ ክርስትና ከመካከለኛው ምስራቅ ወደ አፍሪካ ምድር የገባው በኢትዮጵያ በኩል ነው፡፡ እስልምናውም ቢሆን መንገዱ ይኸው ነበር፡፡

እኛ ድፍን ዓለም እንደሚያውቀን ነው የምናስበው፣ እውነታው ግን ከዚህ የተለየ ነው። ዓለም ስለኛ የሚያውቀው በጣም ውስን ነገር ነው፣ እንደ አታዪ ያሉ ሰዎች ደግሞ ምንም አያውቁም፣ አለያም ስለ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን የሚያውቁት ነገር በጣም የተዛባ ነው፡፡ በዚህ ቆይታዬ ስለራሳችን ያለን ግምት፣ ግንዛቤና አመለካከት ፍፁም የተጋነነ፣ በመረጃ ያልተደገፈና ጠቃሚ ያልሆነ እንደሆነ ተገነዘብኩ፡፡ ኢትዮጵያ የምትባለዋ ሃገር በየትኛው የአፍሪካ አቅጣጫ እንደምትገኝ፣ ምን ደረጃ ላይ እንዳለች፣ የህዝቦቿ ታሪክና እምነት ምን እንደሚመስል፣ ከነጭራሹ ስለዚህች ታላቅ ሃገር ሰምተው የማያውቁ ጋዜጠኞች አጋጥመውኛል፡፡ እነዚህ የመረጃ ሰዎች ለኢትዮጵያ ያላቸው ግንዛቤ ይህን ያህል አናሳና የተዛባ ከሆነ ሌላው ህዝብ ምን ያህል ያውቀናል የሚለው ጥያቄ ውስጤ ተመላለሰ። ለምንድን ነው ዓለም በሚገባ ያላወቀን፣ እኛ ስለምንርቃቸው ነው ወይስ እነሱ ስለማይቀርቡን? ይሄኔ በአንድ መጣጥፍ ላይ ያነበብኩት አንድ ነገር ትዝ አለኝ፡፡ ‹‹ለሶስት ሺህ ዓመታት የዘነጋቸውን ዓለም ዘንግተው ለብቻቸው የኖሩት ኢትዮጵያውያን አሁን ከዘመናት እንቅልፋቸው የነቁ ይመስላሉ›› ይላል፡፡ ፀሃፊው ይህን አባባል የተጠቀመው አሁን እየታየ ያለውን የኢኮኖሚ መነቃቃት ሲገልፅ ነው፡፡ በዛ ስልጠና ላይ የተገኙ ጋዜጠኞችን አመለካከት ለማስተካከል ብዙ ጥሬያለሁ፡፡ ግንዛቤያቸው እንደተሻሻለም እርግጠኛ ነኝ፡፡

ምናለበት ሁሉም ኢትዮጵያዊ በሄደበት ስለሃገሩ ተናግሮ የገፅታ ግንባታ ስራ ቢያከናውን አልኩኝ፡፡ ሃምሳ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክሙ ለሀምሳ ሰው ጌጡ ነው፡፡ በተለይ የኢትዮጵያ ኤምባሲዎችና ቆንስላዎች ስራቸው ምን እንደሆነ ይገርመኛል፡፡ ዋና ተግባራቸው መሆን ያለበት ኢትዮጵያን ለውጩ ዓለም ማስተዋወቅ፣ ንግድና ኢንቨስትመንት መሳብ፣ ለዜጎች ጥብቅና መቆም እንዲሁም ለሃገርና ህዝብ የሚጠቅም መረጃ መሰብሰብ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ በየሃገራቱ የሚገኙ የመገናኛ ብዙሃንን መጠቀም ይገባቸዋል። ሃላፊነታቸውን ጠንቅቀው የተገነዘቡ ግን በጣም ጥቂቶቹ ብቻ ይመስሉኛል፡፡ ይህን ባህል መቀየር አለብን፡፡ ሃገራችንን ማስተዋወቅ ይጠበቅብናል፡፡ በሄድንበት ሁሉ ሁለመናችን ስለ እናት ሃገር፣ ስለ ህዝባችንና ስለ መልካም ባህላችን ይናገር፡፡ ይህ የኢትዮጵያ ጊዜ ነው፡፡

Published in ባህል

የህዳሴ ግድብ አሳሳቢ ውዝግብንና የ“ቢግ ብራዘር” መናኛ ቅሌትን እኩል ያስተናገድንበት ሳምንት

1 ከስደተኛ ኢትዮጵያውያን የሚላክልንን ዶላር እንፈልገዋለን፤ ግን ስደትን በጭፍን እናወግዛለን።

2 መብት ላለመንካት ለወራት ምርመራ እንደተካሄደ በተነገረ ማግስት, ስለ“ቶርቸር” ሰምተናል።

3 የተቃውሞ ሰልፍ በሰላም ተጀምሮ መጠናቀቁን ካየን በኋላ፣ በጠላትነት ሲወነጃጀሉ ታዝበናል።

4 “የነቤቲ የቢግ ብራዘር ጨዋታ” ቅሌት ነው ባልንበት አፍ፣ የወንበዴ ዛቻ እያወረድንባት ቀለልን።

“ግራ የሚያጋባና የሚያደናብር የተደበላለቀ ሕይወት!”… በዛሬው ዘመን፣ የአገራችን ልዩ ምልክት ይመስለኛል። “መደናበርና ግራ መጋባት”፣ ጤናማ ምልክት አይደለም። ነገር ግን፣ ለሺ አመታት ከዘለቀው “ያልተበረዘና ያልተከለሰ የኋላቀርነት ታሪክ” ጋር ሲነፃፀር፣ የዛሬው ሳይሻል አይቀርም።

በትንሹም ቢሆን፣ አሮጌውን የኋላቀርነት ባህል የሚበርዙና የሚያለዝቡ፣ ነገሮች ብቅ ብቅ፣ ጎላ ጎላ እያሉ መጥተዋል። እነዚህን አዳዲስ ነገሮች፣ የህዳሴ ምልክቶች ልንላቸው እንችላለን። ጥሬ ቆርጥሞ ማደርና ዋሻ ውስጥ ተገልሎ መኖር እንደ ትልቅ ስኬት የሚቆጠርበት ኋላቀር ባህል፣ ለስንት ዘመን ስር ሰዶ እንደቆየ አስቡት። አገራችንን እስርስር አድርጎ ለሺ አመታት አላንቀሳቅስ አላላውስ ብሎ የቆየ አሮጌ ባህል ነው። ድህነትና አቅመቢስነት ነግሶብን የቆየውኮ አለምክንያት አይደለም።

ታዲያ አሮጌው ባህል ሙሉ ለሙሉ ባይወገድ እንኳ፣ ያንን የድህነትና የአቅመቢስነት ባህል ጥቂት በጥቂት የሚሸረሽሩና የሚበርዙ ነገሮች ሲገኙ ጥሩ አይደለም? ጥሩ ነው እንጂ። የህዳሴ ምልክቶች ናቸዋ። ለምሳሴ፣ ሕይወታቸውን ለማሻሻል የሚፍጨረጨሩና ቢዝነስ የሚጀምሩ ወጣቶች ትንሽ ሲበራከቱ ካየን፣ የህዳሴ ምልክት ነው። በእርግጥ፣ ድክ ድክ ለማለት እንኳ ያልቻለ እንጭጭ ጅምር መሆኑ አይካድም። ቢሆንም፣ ድህነትን የሚያወድስና የሚያመልክ አሮጌ ባህልን ሊበርዝና ሊያለዝብ የሚችል ቅንጣት የቢዝነስ ባህል ለፍንጭ ያህል መፈጠሩ አይከፋም።

በራሳቸው ጥረት ሃብት አፍርተው በትልልቅ የኢንቨስትመንት መስኮች ትርፋማ የሚሆኑ ባለሃብቶች በየቦታው ብቅ ብቅ ሲሉ ካየን፣ የህዳሴ ምልክት አይተናል ማለት ነው። “የትም ሄደው፣ የሚያዋጣቸውን ሰርተው” ህይወታቸውን ለማሻሻል የሚጥሩ ወጣቶችን ካየንም የህዳሴ ምልክት ነው - ወደ ውጭ አገራት የሚሰደዱትም ጭምር። በአለማቀፍ ደረጃ በሳይንስና በቴክኖሎጂ፣ በቢዝነስና በስፖርት ገንነው የሚወጡ ኢትዮጵያውያን ካጋጠሙን፣ የህዳሴ ምልክት እንዳየን ቁጠሩት - በክለብም ሆነ በብሄራዊ የእግር ኳስ ቡድኖች የምናየው ጅምር ስኬትም ጭምር። ሳይንስንና ቴክኖሎጂን፣ ብልፅግናንና ብቃትን በጠላትነት የሚያይ ኋላቀር ባህልን የሚበርዝ የስልጣኔ ፍንጭ ሲገኝ፣ እልል ባንል እንኳ ፊታችን ፈካ ማለት አለበት። የተቃውሞ ሰልፍ በሰላም ተጀምሮ በሰላም ከተጠናቀቀ፣ የተቃዋሚ ፓርቲ መግለጫ በመንግስት ሚዲያዎች ከተስተናገደም የህዳሴ ምልክት ነው - ሳይወሉ ሳያድሩ አመሻሹ ላይ በጠላትነት መወነጃጀላቸው አልቀረም። አሮጌው የመጠፋፋትና የመጠላለፍ ባህል ገና ምኑም አልተነካማ።

ቢሆንም፣ በአንድ ጥግ በትንሹ ቅንጣት ያህል እንኳ ቢሆን፣ ኋላቀሩን አሮጌ ባህል የሚበረዝ ነገር ሲገኝ፣ “ጥሩ ነው” ማለት ይኖርብናል። የ“ቢግብራዘር” ቅሌትና “የወንበዴ” ዛቻ ሌላው ቀርቶ፣ በ“ቢግብራዘር” ጨዋታ ውስጥ በአህጉር ደረጃ መካፈል የሚችሉ ኢትዮጵያውያንን ማየትም “እንደ አቅሚቲ” የህዳሴ ምልክት ነው። ቁምነገር ኖሮት አይደለም። ግን፣ ቢያንስ ቢያንስ ከጥንታዊው “የሃሜትና የአተካራ ባህል” በመጠኑ እንድንወጣ ያደርገናል። ሳንጋበዝና ሳንጠራ፣ በጎረቤታችንና በስራ ባልደረባችን የግል ሕይወት ውስጥ እየገባን ከምንፈተፍት፣ በሃሜትና በአተካራ የሰዎችን ኑሮ ከምናናጋ፣ የ“ቢግብራዘር” ጨዋታ ላይ ተጥደን መዋልና ማደር እንችላለን። ሕይወታቸውን ከጥዋት እስከ ማታ እየተከታተልን፣ የፈለግነውን ያህል ውሎና አዳራቸውን እያነሳን “በሃሜትና በወሬ” እንድንፈተፍት ፈቅደው ጋብዘውናል። የ“ቢግብራዘር” ትርኪምርኪ ጨዋታ፣ ለኑሯችን የሚፈይደው ነገር ላይኖር ይችላል። ቢሆንም፣ የሃሜትና የአተካራ ሱስ ካለብን፣ ያልደረሰብንና እንድንደርስበት የማይፈልግ ሰው ላይ ሱሳችንን እየተወጣንበት ኑሮውን ከምናናጋ፣ የ“ቢግብራዘር” ውሎና አዳር ላይ ብናወራና ብንነታረክ አይሻልም? በእርግጥ፣ ለሕይወታችን አንዳች ፋይዳ ሳይኖረው፣ የሰዎችን ውሎና አዳር የምንከታተል ከሆነ፣ በዛም አነሰ “የማንወደው” ወይም “የማንስማማበት” ነገር ማየታችን አይቀርም።

ለነገሩ፣ የ“ቢግብራዘር” አዘጋጆች ከመነሻው በግልፅ ተናግረዋል። ጨዋታው… የፆታ ጨዋታንም እንደሚጨምር ገልፀዋል። የፆታ ጨዋታውና ትርኪምርኪው ገንኖ እንደሚወጣ በገልፅ አልነገሩን ይሆናል። ግን፣ እንደዚህ አይነት ዝግጅት ሄዶ ሄዶ መጨረሻው፣ ከዚህ የተለየ አይሆንም። ለምን መሰላችሁ? ሰዎች፣ በሌሎች ጨዋታዎችና ውድድሮች ላይ ተሳታፊ ለመሆን የሚገቡት ለምን እንደሆነ እናውቃለን - ልዩ ብቃታቸውን ለማሳየት ነው - እግር ኳስም በሉት ሩጫ፣ በጥያቄና መልስ ውድድርም በሉት በንግድ ተሰጥኦ ውድድር፣ … የተሳታፊዎቹ ዋነኛ አላማ፣ በልዩ ብቃት ብልጫ ማሳየት ነው። ጨዋታውን የምንመለከተውም፣ የሰዎችን ልዩ ብቃት ለማየት ነው። በቢግብራዘር ጨዋታስ? የተሳታፊዎችና የተመልካቾች አላማ ምንድነው? ነገርዬው የብቃት ውድድር አይደለም። ገመናን አጋልጦ የማሳየት ውድድር ነው። ከገመናዎቹ መካከል፣ የፆታ ጨዋታው ገንኖ ቢወጣ ምኑ ይገርማል? አይገርምም። መጥፎነቱ ያፈጠጠ የወሲብ ጨዋታዎችን ቀርፆ በቲቪ ማሰራጨት፣ ወሲብን የሚያረክስ ቅሌት ነው። ግን፣ ያን ያህልም የምንንጫጫበት ምክንያት አልታየኝም። ምንስ ያንጨረጭረናል? ቅሌቱን መሸከም ያለበት የቅሌቱ ባለቤት እንጂ እኛ አይደለን! እርር ድብን ሳንል፣ “ይሄማ ቅሌት ነው” ብለን ብንናገርና መናኛነቱን ብንገልፅ ተገቢ ነው።

ብዙዎች ግን፣ ከዚያ አልፈው “ከነቤቲ መናኛ ቅሌት” የባሰ፣ “የወንበዴ ክፉ ቅሌት” ውስጥ ገብተዋል። “አሰደበችን፣ ወደ አገር መመለስ አለባት፤ መቀጣጫ እናድርጋት” የሚል ዛቻ በየደረሱበት ሲያራግፉ ሰንብተዋል። “የዛቻ ቅሌት”፣ “ከነቤቲ ቅሌት” የሚብሰው ለምን መሰላችሁ? የነቤቲን ቅሌት እንድናይ፣ እንድንሳተፍ ወይም ሰለባ እንድንሆን በጉልበት ጎትቶ የሚያስገድደን ሰው የለም። ቅሌቱንም ሆነ መዘዙን የሚሸከሙት ራሳቸው ናቸው። “የወንበዴ ዛቻ” ግን፣ ከዚህ በእጅጉ ይለያል። በሰዎች ህይወት ላይ እንዳሻው ለማዘዝና ፈላጭ ቆራጭ ለመሆን የሚቃጣው ሰው፣ የራሱን ሕይወት ብቻ ሳይሆን የሌሎችንም ሕይወት ያበላሻል።

በአጭሩ፣ ያልደረሱበት ሰዎች ላይ ይደርሳል - ምንም ሳይበድሉት ሊደበድባቸው፣ ሊያሳድዳቸው፣ ሊገድላቸው ይፈልጋል - “እረፍ” ብሎ አደብ የሚያስገዛው ህግ ከሌለ። ለእያንዳንዱ ሰው ነፃነት ቅንጣት ታክል ክብር የለውማ። እንዲህ አይነት ሰዎች በአገራችን ብዙ መሆናቸው አይገርምም። ለሕይወትም ሆነ ለነፃነት ብዙም ክብር የማይሰጥ ባህል ለዘመናት ስር የሰደደበትና በኋላቀርነት ሲዳክር የቆየ አገር ውስጥ ነው የምንኖረው። አብዛኛው ሰው፣ ለግለሰብ ነፃነት ክብር ከሌለው፣ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች፣ የመንግስት አካላትና ባለስልጣናትም እንዲሁ በአብዛኛው ለግለሰብ ነፃነት ክብር የሚሰጡ ሊሆኑ አይችሉም።

በአንድ በኩል፣ ስልጣን ሳይኖረን እንዳሻን ሰው ላይ እየዛትን፣ በሌላ በኩል ዞር ብለን፣ “ስልጣን የያዘው መንግስት ነፃነትን የሚያከብር እንዲሆን እንፈልጋለን” ብለን ብንናገር ትርጉም የለውም። ለዚህም ነው፤ “ሰዎች፣ የሚመጥናቸው አይነት መንግስት ይኖራቸዋል” የሚባለው። መብታችንና ነፃነታችንን የሚያከብር መንግስት እንዲኖረን ከፈለግን፣ በቅድሚያ ለእያንዳንዱ ሰው መብትና ነፃነት ከፍተኛ ክብር የምንሰጥ መሆናችንን ማረጋገጥ ይኖርብናል። ያኔ በህዳሴ ጎዳና (በስልጣኔ ባህል) ላይ ትልቁን እርምጃ ተጓዝን ማለት ነው። የህዳሴን ጅምር ከአሮጌው ባህል ጋር እያደባለቅን ከመደናበር የምንላቀቀውም ያኔ ነው። የሙስና ምርመራና የ“ቶርቸር” ምርመራ ከሳምንታት በፊት፣ የፀረ ሙስና ኮሚሽን ለፓርላማ ባቀረበው ሪፖርት ላይ፣ በሙስና የተጠረጠሩ ባለስልጣናትን ከማሰሩ በፊት ለበርካታ ወራት ምርመራ ሲያካሂድ መቆየቱን ገልጿል። ምርመራው ለምን ያን ያህል ጊዜ እንደፈጀ ተጠይቀው ኮሚሽነሩ ሲመልሱ፣ የአንድም ሰው መብት መነካት ስለሌለበትና አስተማማኝ ማስረጃ ማሰባሰብ ስለሚያስፈልግ የበርካታ ወራት ምርመራ መካሄዱን ተናግረዋል። እንዲህ አይነት አስተሳሰብ፣ የህዳሴ ምልክት ነው። በሁሉም የመንግስት ተቋማት ውስጥ በተለይም በፍትህ አካላት ውስጥ በስፋት ልናየው የሚገባ ስልጡን አስተሳሰብ ነው፤ በንግግር ብቻ ሳይሆን በተግባርም ጭምር።

አሳዛኙ ነገር፣ በርካታ ተጠርጣሪዎች ከታሰሩ በኋላ ወደ ፍርድ ቤት ሲቀርቡ፣ በርካታ አሳሳቢ አቤቱታዎችን አቅርበዋል - ከህዳሴ ጋር የሚቃረን አሮጌው ባህልን የሚጠቁሙ አቤቱታዎች። ከጠበቃ ጋር ለመገናኘት መቸገራቸውን የተናገሩ እንዳሉ ሁሉ፣ ድብደባ እንደደረሰባቸውና “ወተር ቦርዲንግ” የሚባለው ስቃይ እንደተፈፀመባቸው የገለፁም አሉ። ሰሞኑን ደግሞ፣ ከተጠርጣሪዎቹ መካከል አንዷ፣ በውድቅት ሌሊት እራቁቴን ቀዝቃዛ ውሃ እየተደፋብኝ ምርመራ ይደረግብኛል በማለት ለፍርድ ቤት አቤቱታ አቅርበዋል። አቤቱታ ሲቀርብ፣ እውነቱን ለማረጋገጥ፣ እውነት ሆኖ ከተገኘም ተጠያቂውን ሰው ለማወቅ ምርመራ መካሄድ እንዳለበት ግልፅ ነው። ፍርድ ቤቱ የሰጠው ትዕዛዝም ይህን የተከተለ ይመስላል። በስልጣናቸው አላግባብ ተጠቅመዋል (ሙስና ፈፅመዋል) ተብለው የተጠረጠሩ ሰዎች ሲታሰሩ፣ ተጠርጣሪዎቹን እመረምራለሁ ብሎ ስቃይ የሚፈፅምባቸው ከሆነ ስልጣኑን አላግባብ እየተጠቀመ (ሙስና እየፈፀመ) ወንጀል እየሰራ ነው ማለት ነው። በእርግጥ፣ የፖሊስም ሆነ የፀረሙስና ኮሚሽን ተቋማት፣ “እስረኛን አናሰቃይም” በማለት እንደሚያስተባብሉ አይካድም። ጥሩ፤ ተጠርጣሪዎችን ማሰቃየት እንደ ትክክለኛ የምርመራ ዘዴ እንደማይቆጥሩት መናገራቸውም አንድ ቁም ነገር ነው።

ነገር ግን፣ እንዲህ አይነት አቤቱታዎችን በጠላትነት አይን ማየት የለባቸውም። አንደኛ ነገር፣ የፖሊስ ዋና አላማ፣ ህግ ማስከበርና የሰውን መብት ማስጠበቅ ነው። አቤቱታ ሲቀርብ፣ በቅንነት ተቀብለው ማጣራትና ምርመራ ማካሄድ አለባቸው። ሁለተኛ ነገር፣ ተጠርጣሪን ማሰቃየት እንደ ትልቅ ጥፋት ወይም እንደ ወንጀል የማይቆጥሩ ብዙ ሰዎች ባሉበት አገር፣ የፖሊስ አባላት በሙሉ በጭራሽ ተጠርጣሪን ለማሰቃየት የማይሞክሩ እንከን የለሽ ቅዱሳን ናቸው ብሎ መከራከር የትም አያደርስም። ሞባይል ሲሰረቅበት፣ የሚጠረጥራቸው ሰዎች ሁሉ ታስረው እየተቀጠቀጡ እንዲመረመሩለት የሚፈልግ ሰው የሞላበት ኋላቀር አገር ውስጥ ነው የምንኖረው። ይህንን አስተሳሰብ የሚከተሉ ፖሊሶች ቢኖሩ ምን ይገርማል? ሞልተዋል። ይህንን ለማስተባበል ጊዜ ከማባከን ይልቅ፣ አገሪቱ ከአሮጌው ባህል ተላቅቃ በህዳሴ ጎዳና እንድትራመድ የሚያግዝ ጥረት ላይ ብናተኩር ይሻላል። ለዘመናት የዘለቀውን ኋላቀር ባህል በአንዴ መለወጥ ባይቻልም፣ በየጊዜው የሚቀርቡ አቤቱታዎች ላይ ምርመራ በማካሄድ ቀስ በቀስ ስልጡን አስተሳሰብና አሰራር እየተስፋፋ እንዲሄድ ማድረግ ይቻላል።