Saturday, 15 June 2013 11:46

እማይነትበዉ ስዉር-ስፌት

ክፍል ሁለት፥ በጥሞና ስለአራት ግጥሞች

፩ ሀገርህ ናት በቃ ! 

አያሌ ገጣሚያን ሀገር ስትፈካ፣ ሀገር ስትፋቅ፣ ገሃድ ሲገጣጠብ ወይም ሲያብረቀርቅ ግለሰቡ እኔ ምን አገባኝ የመሰለ ገለልተኝነት እንዳይጠናወተዉ ተቀኝተዋል:: ስለ አገር ያልፃፈ የአማርኛ ገጣሚ የለም:: ብዙዎቹ በፍቅር በናፍቆት፣ ጥቂቶቹ እየረገሟት፤ እንደ ወዳጅም እንደ ደመኛም:: ሆድ የባሰዉ፣ ያቄመ፣ ተገፍትሮ ዉስጡ ያመረቀዘ ለሱ <ሀገር> ምኑ ናት ? ያምፅ ይሆናል ወይም ይስለመለማል:: አገር ሲባል ግዑዙ ብቻ ሳይሆን ማኅበረሰቡ፣ ባህሉ፣ ዕምነቱ፣ ወዳጅና ዘመድ ... ይጠራራሉ:: ስብሐት በ <አምስት ስድስት ሰባት> አጭር ልቦለዱ የገለፀዉ በርሱፈቃድ <... ሰሞኑን ስለ ክርስቶስ ስቅለት ትሰማላችሁ:: ግን ማነዉ ሰዉ ሆኖ ያልተሰቀለ? ማነዉ በልጁ ለቅሶ ያልተቸነከረ? ማነዉ በሚስቱ ሞት ያልተቀበረ? ... ከነልጆቹ ረሃብ ሲከታትፈዉ ለሀገርም ለስቅለትም ህሊናዉ ይሻክራል::

እንግዲህ ባለቅኔ የት ሆኖ? ገጠመኙ ምን ቋጥሮ ፃፈ ? የግጥሙ ተናጋሪ personna ንቃተ ህሊናዉ እንደነገሩ ነዉ ወይስ ተመስጧል ? ዘመነኛ ሂስ ፅሑፍን እንጂ የወቅቱን መንፈስና የባለቅኔዉን ግለታሪክ ማሰስ አያደፋፍርም:: ነቢይ ከአማርኛ ገጣሚያን የሚለየዉ አንድ-ሁለት ሳይሆን፣ በአገር ጉዳይ ከሃያ ግጥሞች በላይ መቀኘቱ ነዉ:: የኛ ሰዉ በአሜሪካ መፅሐፍ ልዩ ጣዕሙ ስለ አገር ቤት ትዝታ፣ ኑሮ፣ ህልም ... እያጠለለ ገፆቹ ርሰዉ ስላፈሰሱም ነዉ::
ግለሰብ እትብቱንና ስሩን የተቀማ ተንሳፋፊ እንዳይሆን ይሰጋል:: ሥነቃሉም <አገር አላት ይበሉኝ፣ ማህደረ ማርያም ቅበሩኝ> ሲል የስፍራ፣ የማንነት ጥያቄ ከአፈር ጋር ይቦካል:: ነቢይ “ባገር የመሸ ቀን፣ ሰዉ አገር አይነጋ // ማብቃቱ ታወቀኝ ሲደርስ አፈሯጋ” እንዳለዉ ነዉ:: ሰለሞን ደሬሳ በዘበተ እልፊቱ መግቢያ፣ ከጠፉበት ብዙ ግጥሞች < ... ሆዴን የምትበላኝ አንዲት በኤርትራ ነፃነት ማግስት የፃፍኳት ወለሎ ብቻ ናት::
...ታሪክን ለማበጠር የማትሞክር፣ አርበኝነት የማይጐድላት፣ ጀግና የማይፅፋት፣ የግል ሀዘኔ የተጫናት ወለሎ ብቻ ናት::> ብሏል፤ አገርም ፀፀትም ተሸራርበዋል:: በድሉ ዋቅጅራ በኤርትራ መገንጠል ማግስት <ለካስ መሬት እግር አለዉ!> እያለ በግጥሙ ተመስጧል:: [ፍካት ናፋቂዎች፥ 45]
“እንደ አላቂ ብጣሽ ጨርቅ፣ መርፌ ላይጠቃቅመዉ / እንደ ባልና ሚስት ጠብ፣ ገመና ላያግደዉ / አይሄድም ሲሉት ይሄዳል፤ ቅርብ ነዉ ሲሉት ይርቃል፤ ለካስ መሬት እግር አለዉ::” ብድግ ብሎ የሚኮበልል ስፍራ ያስደነግጣል:: ከመንደሩም ተፈናቅሎ ሀገሩ ዉስጥ ሌላ ቦታ የሚሰፍር ከባዕድ አገር የተሰደደ ይመስለዋል:: የቆሌ፣ የአድባር ዛፍ፣ የታቦት... ቁርኝት ነዉ::
ወጣት ገጣሚያን በሀገር ጉዳይ ዕምቅና ዉስብስብ መሆን ይደፍራሉ:: በዕዉቀቱ ሥዩም <የመፅዋተኛዉ አገር> በማለት ህሊናን ይቦጫጭራል:: “አገር ድንኳን ትሁን /ጠቅልዬ የማዝላት/ ስገፋ እንድነቅላት /ስረጋ እንድተክላት::” እንደ ሁኔታዉ የሚኮሩባት አሊያም የሚሸሽጓት ሀገር:: ኑረዲን ዒሳም በተነበበ ቁጥር ቀንበጥ ፍካሬ የሚለግስ ግጥም ተቀኝቷል:: “አንድ ትልቅ ሃገር፣ በትንሽ መንደር ላይ / ተጣጥፎ ተኝቶ / ሲጨናነቅ አየሁ፣ ለእግሮቹ መዘርግያ / ሽራፊ ቦታ አጥቶ::” አገርን ትንሽ ስፍራ ዉስጥ ማስጨነቅ ሳይበቃ <የክፉ ዘመን ህልም> በማለት ዋሲሁን በላይ አመረረ:: “አገሬን / ኮሮጆ ከትቼ / በምስማር መትቼ / ከቆጥ ላይ ሰቀልኋት፣ /ነግቶ ስፈልጋት/ መርዝ በበሉ አይጦች /ተበልታ አገኘኋት!” እንደ ፅላት ታቦት ዉስጥ መደላደል ያለበት ሀገር፣ ከጨርቅ ከቁርበት በሚስሰፋ የሆነ ዕቃ የሚቋጠርበት ኮሮጆ ዉስጥ ተሸብልሎ ጉድ ሆነ:: የሚያሳምም ርዕስና ግጥም ነዉ::
ነቢይ አገርን ከስደት፣ ከባይተዋርነትና ከናፍቆት እየነከረ ያስተዉላል:: ሆድ የባሰዉ ወይም ሩቅ አላሚ ቢሰደድ ሌጣዉን አይደለም፤ ትዝታዉን፣ ልጅነቱን፣ ፍቅርና ጥላቻዉን ከዉስጡ አምቆ ነዉ የተጓዘዉ - የነተበ ዘባተሎ ይመስል አወላልቆ አይሄድም:: ላለማስታወስ፣ በሌላ ጉዳይ መጠመድ ቢሞክር ትናንቱ ድቅን ይልበታል:: “ኧረ አንድ በሉት በበለስ፣ ይሄ የአገሬ አፈር ደሞ / ኋላ ረገጥከኝ እንዳይል፣ አጉል መንገዴ ላይ ቆሞ” ነቢይ በሁለት ሀይል እየተጐተተ፣ ስደት ቢደላዉም አገሩ እያባነነዉ ስለተሰቀቀ ግለሰብ ተቀኝቷል:: ማን ያስጥለዉ፣ ማን እንዲቀናዉ ይዘክረዉ? ለንባብ የተቀነበበዉ ግጥም “አገርህ ናት በቃ !” ቁጥር ሁለት ነዉ:: በቁጥር አንድ ጠበኞችን ይገላግላል:: “ይቺዉ ናት ዓለምህ፤ ብቻዋን የተኛች ከዓለም ተደብቃ // ልቧን አታዉልቃት አትጨቅጭቃት በቃ / አብረህ አንቀላፋ ወይ አብረህ ንቃ” ቁጥር ሁለት ረቀቅ ይላል፤ መገላገል ሳይሆን መሳተፍ፣ ለጋራ የግልን መጋረድ፣ ትንሳኤን ማጣደፍ ይመስላል:: በሶስት አንጓ ሊከፈል የበቃ ግጥም ነዉ::

አንዳንዴ፤
አንጐሌን እንደዣንጥላ አጥፌ
አገሬን በወግ ሰልችቼ፣ ፍቅሯን ከልቤ አጠንፍፌ
ወደሷ የሚያደርሱኝን፣ መንገዶቼን ሁሉ አጥሬ
ሌላ ሌላ አገር አያለሁ::
አንድም አገሩን ገፍትሮ ባህር ለመሻገር የተነሳሳ፣ አንድም ለሀገር ያባዉን በጐ ስሜት ሆን-ብሎ ለማስተባበል የሚጣጣር፣ አንድም እርግጠኛ ለመሆን የሚታክት ሄደ-ቀረ የምንለዉ ተናጋሪ ጥርጣሬዉን ይናዘዛል:: < አንዳንዴ > ማለቱ ግን ሀገርን ቸል በሎ ለመራመድ የሰርክ ግፊት እንዳልሆነ ይጦቅማል፤ በአመዛኙ ዕርቅ ላይ ነዉ ወይም አላቄመም:: ማሰሮ ዘቅዝቆ የአገር ፍቅሩን ያፈሰሰ መስሎታል:: ይህ አንጓ የተናጋሪዉን መደናገር፣ በዕዉኑ ራሱን ከአገሩ እየጋረደ ለመገለል፣ በደመነፍሱ ግን ሰለቸዉ እንጂ አልተበደለምና መስቀለኛ መንገድ ላይ ዉል ጠፋዉ:: ሆኖም ቆዳዉ ስስ አይደለም:: ስንት የጋለ የእምባ ጠብታ ፈገግታን ያገነፍላል? ጥማት የሚያጋልጠዉ የምንጭ አሰሳ መሰለ:: ገና የሚጤን እሚያማክሩት ከልብ ዉስጥ የተሰነቀረ አንዳች ነገር ቀርቷል:: <ተስፋ ያልቆረጠ መነኩሴ ምናኔ ሲሄድ ሴቲቱን ይሰናበታል> የመሰለ ማቅማማት ነዉ:: ለመሄድም ለመቅረትም አንድ ድርጊት መከሰት አለበት::

አገሬ ግን፤ ...... እንደጌታ የስቅለት ቀን
በአራት አቅጣጫ ተወጥራ
እመስቀል ላይ ተቸንክራ
ጣሯን ቁልቁል በማሰማት
ነገዋን በእኔ ለማየት
“ላማ ሰበቅታኒ ?” አለችኝ - “ለማን ተዉከኝ በዚህ ሰዓት ?”
ፊቴን መልሼ አየኋት::
የምር ሆነ፤ አገር ልጆቿን ትማጠናለች:: ይህ ምስል ግን - የጌታ ስቃይና ሕማማት - ክህደትንም ያስታዉሳል፤ አሳልፈዉ የሰጡትን:: የአገር ትንሣኤ እንደ ጌታ ትንሣኤ የተረጋገጠ መሰለ:: <ኤሎሄ ኤሎሄ ላማ ሰበቅታኒ ?> አምላክ ትልቁን አምላክ ሲማፀን አያዎነቱ ፈተና ነዉ:: ከመጥበብ ይልቅ የሚሰፋ ክፍተት አይነት:: ደራሽነቱ ቅፅበታዊ፣ ያኔዉኑ ግን አይደለም:: ሰለሞን ደሬሳ ስለ አንድ ግጥሙ ሲተች ለአገር ምላሽ ወድያዉነትን አደመቀ:: አገር፣ ጠላት ድንበሯን በጉልበት ከሰበረ ታቃስታለች:: አዳል ተሰማ ሰራዊት አስከትለዉ ወሰን ጥሶ የመጣዉን የደርቡሽ ጦር ግንባር ለግንባር ገጥመዉ ኑሮ፤ ድል መመታት መጣ:: ሀበሻ ግልብጥ ብሎ ሲሸሽ ... ተገኝ ወርቄ የሚባል ስመ-ጥር የጐጃም ፈረሰኛ በግር የምትሸሸዉን የዛለች አረሆ በፈረስ ሲያልፋት <አዙር ተገኝ በንጉሥ ሞት> ብትለዉ ፋታ አልሰጥ ብለዉ ከነበሩት ደርቡሾች ጥቂቶቹን ገድሎ ዘፋኟን አፈናጠጣት:: ፈረሰኞቹም <አዳልን አናስበላም> በማለት አሸናፊዉን ደርቡሽ የድል ሰዓቱን አስረገሙት:: [ልጅነት፥ 77]
የጌታ መስቀል ላይ መቸንከር ለሀገር ተምሳሌት፣ ፅልመትም ተስፋም ነዉ:: ነጋ ጠባ ሽሽት ላይ ያለ ግለሰብ፣ እግዜር በየቦታዉ የሚያሯሩጠዉ ከመሰለዉስ? በደረሰበት በደል ሳቢያ ጀርባዉን ለጌታ የሰጠ፣ ጌታን ለሀገር አይታመንም ካለስ ? ኅሩይ ወልደ ሥላሴ የሚተርከዉ አለዉ:: ሁለት ባሎቻቸዉ የሞቱባቸዉ ሴቶች ነበሩ:: አንዷ ባለወገን የሁለት ልጆች እናት፣ ሌላዋ የአንድ ልጅ እናትና የቸገራት:: በሽታ ገብቶ የመንደር ልጆች ታመሙ:: ባለወገን ልጆቿ ዳኑ፤ ድሃዋ ግን ልጇ ሞተ:: <...የጐንደር ሴቶች ሳይማሩ የተማሩ ናቸዉና እናት እንዲህ ብላ አለቀሰች “ሁለቱን ታማለህ አንዱን ትገድላለህ፣ / የሴት ልጅ ነህና ፍርድ ወዴት ታዉቃለህ ?” [የልቅሶ ዜማ ግጥም፥ 11ኛዉ] እንዲህ ምርር ያላት እንስት የጌታ ምስል አይመጣላትም:: በአራት አቅጣጫ መወጠሩ አይገባትም:: ቅን ካልሆነች የሩቁን አታጤንም:: የነቢይ ግጥም ተናጋሪ ግን የሀገሩን ማጣጣር አድምጦ መስዋዕት ለመሆን የተዘጋጀ ነዉ::

ሩቁን የአንጐሌን ዣንጥላ፣ መልሼ ዘረጋሁላት
አፈሯን ጠርጌ ቁጭ አልኩ፣ ትንሣዔዋን ላልምላት!!
ይች ናት አገሬ ማለት
ሞታ እስከምትነሳ፣ ተኝታ እስከምትነቃ
አገሬ እችዉ ናት በቃ !!
የተበረከተዉም - ለአገሬና ለህልሜ- ነዉ:: ተናጋሪዉ ከራሱ ጋር የሞገተበት ያልተንዛዛ ተራኪ ግጥም ነዉ:: ሀገርን ከጐህ እስከ ጐህ ከመዉቀስ፣ በአገር ከመሸማቀቅ ማለምና መጠበቅ የተመረጠበት ነዉ:: ሌላዉ ቢቀር <አፈሯን መጥረግ> አሀዱ ተግባር ነዉ:: ግጥሙም የተጠነጠነበት ምስል ተራ ስቃይና ጩኸት ሳይሆን ሀያሉ ጌታ - እንድ አገር - የራደበት ነዉ:: ለዚህም ነዉ ተናጋሪዉ “ቁጭ” ብሎ እንዳይቀር የሚያሰጋዉ:: የደበበ ሰይፉ <ከአክሱም ጫፍ አቁማዳ> ያስታዉሰናል፤ ሀገር ተርቦ ለአንድ ቁና ጤፍ ብድር፣ ባዶ ተልኮ ሌጣዉን የተመለሰ የተጨማደደ አቁማዳ። ከባዶ አቁማዳ የሚዛቅ የሀገር ፍቅር፤ ይህ የአገር ጥሪ ከግለሰብ ኩርፍያ የላቀ የመጠቀ ነዉ:: ነቢይ ተኝታ አትቀርም-ትነቃለች የመሰለ ተስፋ ነዉ ያከረረዉ:: ባዕድ ጠላት አገራችንን ከገላመጣት ህዝብ አይጠብቅም፤ ይዘምታል:: የእርስ በርስ ትንቅንቅና ጠብ፣ አገርና የአገር ልጅ መኮራረፍ ግን የተለመደ ነዉ:: በብዙ ምክንያት ባህር መሻገር፣ ከመንደር መራቅ አለ:: ሥነቃልም ይህንን ዕዉነታ ይቀባበላል:: “እኔ መሄዴ ነዉ ሄድኩልሽ ከሀገር / ሰፌዱም እንቅቡም ጠምዶኛል በነገር” ከተሰደዱ በኋላ ነዉ ልብ ዉስጥ ያንቀላፋዉ ሀገር ተቀስቅሶ ያዙኝ ልቀቁኝ የሚለዉ:: አገር ላማ ሰበቅታኒ ብላ ስትማፀን ብድግ ብሎ የሚሸሽ ግን ወጨት ሰባሪ ነዉ:: <የግልብጥ ሩጫ> ይለዋል ነብይ::

ይገርማል ...
ስንት አይነት ችኩል ሰዉ አለ
መሮጥ መንደርደሩን በቀር፣ መድረሻዉን ያልታደለ::
ለአገር ማቃሰት፣ መነሳሳት እንጂ ጀርባ መስጠት ማስተዛዘቡን በዉብ ምስሎች ያደነደነ ግጥም ነዉ::

፪ ነገሩ ገብቶኛል [ ስዉር-ስፌት ፥ 85 ]
ጠዋት ቤትሽ መጣሁ
አንቺ ግን የለሽም፤ በተስኪያን ሄደሻል::
ያዉ፤ የገላገልሽዉ
የጉደሩ ጠርሙስ ባዶዉን ተኝቷል::
ስትንፈራገጪ ድንገት የረገጥሺዉ
ብርጭቆ ተሰብሮ፣ ወለሉን ሞልቶታል::
ብርድልብስሽ የለም -
እንደአድፋጭ - ዉሽማ፣ አልጋሽ ሥር መሽጓል::
አንሶላሽ ከፍቶታል -
በሌሊቱ አበሳ ሽንሽን ቀሚስ መስሏል::
ግድየለሽም ፍቅሬ ነገሩ ገብቶኛል
በህልምሽ ከኔ ጋር፣ ተቃቅፈሽ አድረሻል::
እኔ አኩርፌሽ ብዬ፣ ጅሉ ልቤ ወልቋል::

አይ የልብሽ ጉዱ !
ዕምነትን መሻሩ፣ ልማድን መካዱ
ለብቻ እንዳደረ፣ ደሞ እንደጨዋ ልብ፣ በተስክያን መሄዱ::
አይ የልብሽ ጉዱ !
ያፈቅራታል፣ ግን ተቀይሟት ብቻዉን ከቤቱ አደረ:: እስክታባብለዉ አልጠበቀም፤ ማለዳ ከቤቷ ቢመጣ ጉድ ሆነ:: ሌሊት የጦፈ የተረማመሰ ወሲብ የተጐዘጐዘበት አልጋ ጠበቀዉ:: አምሮት እያቃሰተ ከህይወት ጣፋጭ ጣዕም እንዴት ይላቀቅ ? የተወራጩበት ሌሊት ሌጣዉን አልነጋም፤ የተራረፈዉን ፍራሽ ላይ በታትኖ ነዉ የሄደዉ:: ይህን ግጥም ደረጀ በላይነህ ቃኝቶታል <በዚህ ግጥም አልጋ እንደ መፅሐፍ ተገልጦ ይነበባል፤ ይተረካል... ከህይወት ፍቅርን ገልብጦ እንደጥጥ ሲከምረዉ ጉድ ነዉ::> [ ብሌን ቁ5 ፥ 37 ] ይህ ግጥም የተጨረማመተ ታሪክ ሸሽጓል:: ገጣሚዉ ለአፍታ ከተናጋሪዉ ጋር አገጣጥሞን ገሸሽ ይላል:: አይኖቹን እንደ ካሜራ እያዟዟረ የፍቅረኛዉን መኝታ ክፍል ይታዘባል:: ትናንት ምን አጣላቸዉ ? በጧት ምን ፍለጋ ከቤቷ ሰተት አለ ? የሴቷ ፅላሎት ረበበ እንጂ ድምፅዋ አይሰማም:: ከወንዱ አንፃር ነዉ የተቀረፀዉ:: ሆኖም ገጣሚዉ በሚመስጥ ምስል ያነዘራቸዉ ስንኞች ሌላ ሌላም ይናገራሉ:: በሩ የወላለቀበት ግጥም ሳይሆን ተጨማሪ ስዉር ጓዳ አለዉ::
ከመኝታ ክፍል ትዕይንት ይልቅ እጅጉን የሚመስጥ ተናጋሪዉ ነዉ:: አልጋ ስር ሳይቀር ያሰሰዉን ዕዉነታ ይክዳል፣ ወደ ዉስጡ ሊያፈገፍግ፣ ሊኮራመት መሆኑ ያስታዉቃል:: እሷ በሌለችበት እየተናገረ፣ ያየዉን እንደፈለገዉ ነዉ የተረጐመዉ:: አንድ አይኑ ያስተዉላል፤ ሁለተኛዉ በአሳብ ይቃብዛል:: የሌላ ወንድ ጠረንና አሻራ ፍለጋ የተኛችበትን አልጋና ዉስጥ ልብሷን በአይኖቹ ይሄድባቸዋል:: ራሱን ያፅናናል፤ “በህልምሽ ከኔ ጋር፣ ተቃቅፈሽ አድረሻል” እያለ:: ተናጋሪዉን ማመን ይቻላል ወይ ? የተደረገዉን፣ የተፈፀመዉን ሳይሆን እሱ ስሜቱን ለማስከን የልቡን ሸሽጐ የአንደበቱን ያወጋ ይመስላል:: መኝታ ክፍሏን ሳታስተካክል ምን አጣድፎ አስወጣት ? አፍቃሪዉ ክህደቷን ለምን አለዘበዉ ? ይህን ክፍተት አንባቢዉ እንዲሞላዉ ነዉ የተተወዉ:: ነቢይ ግጥሙን አለወትሮዉ በመንቶ ነዉ የቀረፀዉ፤ ስንኞች እየተቀባበሉ ግጥሙን አይዘልቁም:: በሁለት በሁለት አንድ ትዕይንት እየላጡ አረፍ፣ ሰከን፣ ቀጥ ይላሉ - የተናጋሪዉን ማቃሰት እያረገቡ:: ተራ በተራ ብርሃን የሚዞርበት የአልጋ ጠርዝ የሚቋጨዉ በከፊል የተናጋሪዉን ሥነልቦናና የዋህነትን አቀጣጥሎ ነዉ:: ገጣሚዉ - በዕዉን ያጡትን በሕልም ለሚያገኙ - ብሎ ግጥሙን ስለአበረከተ የተናጋሪዉን ድምዳሜ አድምቆ ይሆናል እንጂ፣ ገለጣዉ ከማታ ድርጊት የተረፈን ዕዉነታ፣ በፍቅርና በወሲብ መካከል ያለዉን የሀይል ልዩነት ሳያድበሰበስ ይጦቅማል::
በቃል ግጥም የተጠቀሰዉ የእንስቷ ስጋዊ ፍትወት አልተገደበም “ወየዉ ባደረገኝ የደጅህን ሰርዶ / አህያህ በበላኝ ጐራርዶ ጐራርዶ”:: አንዳንዴ እንስት የሚመዘምዛት የወሲብ ረሃብ ይሰፍርባታል፤ ወንዱ ደግሞ እንደነገሩ ሊሆን ይችላል:: ደምሴ ፅጌ በፍለጋ ልቦለድ የቀረፃት ቅድስት፣ እንዳለጌታ የወሲብ ጥሟን የተቀኘላት የዛጐል ልቦለድ ዕሌኒ ይታወሳሉ:: ወሲባዊ ጥሪዋን የግጥሙ ተናጋሪ ያጤነዉ ይመስላል:: አፈቀራት እንጂ የዕዉነታዉ ስቃይ እንዳለ ነዉ፤ ከሌላ መቅበጧን ማስተባበሉ አዝግሞ እንዲጓዝ አግዞታል:: “እምነትን መሻሩ፣ ልማድን መካዱ / ለብቻ እንዳደረ፣ ደሞ እንደ ጨዋ ልብ፣ በተስክያን መሄዱ” ሲል ለገሃድ እንጂ ለህልም እንዳልሆነ ልቦናዉ ያዉቃል:: የበድሉ ዋቅጅራን ባለ አንድ መንቶ ጥልቅ ግጥም ያስታዉሰናል::

እኔ ምኑን ተጐዳሁ፣ ላንቺ ይብላኝልሽ እንጂ
እንደ መንፈስ ዉስጤ ሳኖርሽ፣አካል ሆነሽ ስትሄጂ

ግጥሙ ዉስጠቱ የተጋረደ ግርማነት ያጠላበት ነዉ:: እሱ እንደ መንፈስ እየሸበለላት፣ እሷ ከስዕሉ ሸራ ወርዳ ርቃዉ ትሄዳለች:: መመለክን የመሰለ ፍቅር ሳይሆን፣ መተሻሸትና የአካል ግለት እርቧት ከሆነስ ?
<ነገሩ ገብቶኛል> ግጥም ሲጤን አፍቃሪዉ ከመኝታ ክፍል ያየዉን በደረቁ አልገለጠም:፡ ከዉስጡ፣ ከታህተንቃቱ - subconcious - የሸፋፈነዉ የሚላወስ ጉዳይ እያፈተለከ በምስል ይከሰታል:: በመተሻሸት ሽንሽን ቀሚስ የመሰለ አንሶላ፣ እንደ አድፋጭ ዉሽማ አልጋ ሥር የመሸገ ብርድ ልብስ ... ገላዋን ባዕድ እንደሚጋራዉ ነግረዉታል:: እሱም ከአካሏ የሚቀስመዉን ላለመነፈግ ይመስላል የሚያስተባብለዉ:: ገመና፣ ምስጢር እንዲሆንለት ነዉ ገሀዱን በህልም የሚመነዝረዉ:: <የየጁ ቄስ ቅኔዉ ቢጐድልበት፣ ቀረርቶ ሞላበት> አይነት ግን አይደለም፣ ተናጋሪዉ ሆን ብሎ ነዉ የደበቀዉ:: <ትንፋሽሽ አይራቀኝ አቦ !> የሚለዉ የነቢይ ግጥም ተናጋሪና ይህ የፍቅረኛዉን አልጋ የሚበረብር አፍቃሪ አንድ ናቸዉ:: በሩቅ መሆንን መርጠዋል::

ሲበርደኝ
ወደ አንቺ እደዉላለሁ
ድምፅሽ ዳር ቁጭ ብዬ
እንደሳት እሞቃለሁ::
የፍቅርና የወሲብ ጣዕም እንደ ግለሰቡ ይበላለጣል:: የከአድማስ ባሻገር አበራ ወርቁ - ባህር ማዶ ተምሮ የጨመተዉ - እንኳን፣ ሉሊት የከዳችዉ መስሎት የአልቤርጐ በር በርግዶ ሌላ ሴት በጥይት ገድሏል:: ነገር የገባዉ አፍቃሪ ግን ክህደቷን አስተባብሎ እንዳትፈርጥበት ያዝላታል:: እንደ አላል - አላል የተጫነዉን ጭነት ለማስተካከል፣ በላዩ ላይ የሚደረብ ተጨማሪ ጭነት ነዉ፣ አለበለዚያ ይሰናከላል:: ክህደቷን ለመጀመሪያ ጊዜ ያጋጠመዉ ሣይሆን የተለማመደዉ ይመስላል:: ይልቅስ የተጐዳችው እንስቷ ናት:: ሲያከንፋት ያደረ የወሲብ እርካታ ትዝታዉ ሳይተን፣ ፍቅረኛዋ በህልምሽ እኔን አቅፈሽ አድረሻል ቢላት ትሸማቀቃለች:: ወይም ለክህደቷ ንሰሃ ልትገባ ጧፍና ዘቢብ ዘግና ቤተክርስትያን ሄደች፤ እንዳይታወቅባት ትሳላለች የመሰለ አንድምታዉን ብታጤን ሊሰቅቃት ይችላል:: ለአንድ አጭር እድሜ በሱም ዉስጥ ላለዉ ዉስን ትኩስነት መኖር፣ ሊያላትም ይችላል:: ወንድ በፍቅር ለፈዘዘላት እንስት እያቃሰተ፣ እየተደናቀፈ ማዝገም መምረጡን ነዉ ነቢይ የተቀኘዉ:: ድሮም ቢሆን በጨሌና በገንፎ የምትከበር የሴት አምላክ አቴቴ ናት::

፫ ብቸኝነት የተደሰተበት ቀን [ ስዉር-ስፌት ፥ 113]
ጐዶሎ ... የቡና ብርጭቆ
ግማሽ የነደደች ክብሪት
ግማሽ የጨሰች ሲጋራ
አሽትሬ ከቁሩ ጋራ::
ቡና የደረቀባት ማንኪያ::
ጉስቁልቁል ያለ ሰዉዬ፣ ኑሮ እንደሸሚዝ ያለቀበት::

ሰዉዬዉ፤
ከነሃሳቡ፣
ከነሰባራ ኮከቡ፤
ባንዳች ስሜት ያላንዳች ቃል
ከብቸኝነት ይጫወታል::

ቆየ ቆየና ግና፤

ሲጋራዋን ስቦ ስቦ፣ ከምሬት ጋር ወረወራት
በጥቁር ያለቀ ጫማ፣ ወለሉ ላይ ደፈጠጣት
አጅሬ ብቸኝነትም፣ ጮቤ ረገጠ ክልቡ ፍንድቅድቅ አለ በሀሴት
ባደባባይ ግዳይ ጣለ፣ አ.ን.. ድ ጠላት ወደቀለት !
ግለሰብ ሲያዉጠነጥን፣ሲቀፈዉ ወይም በሆነ ጉዳይ ከታወከ ተለይቶ ለብቻዉ መነጠልን ይመርጣል:: ነቢይ የብቸኝነት መብት ይለዋል:: በሀገር ልብስ ደምቀዉ ለረበሹት አዛዉንትና ግለ-ነፃነት ላጡ የተቀኘዉ ነዉ:: “ስጡኝ አንድ ጥጋት / አንዳንዴ የማርፍበት / እንደ ዕዉነት የምትሞቅ / እንደ ዉበት ደማቅ” [ ጥቁር ነጭ ግራጫ ፥ 31] በስዉር-ስፌት ስብስቡ “ዘላለምን ካፍታ አባርቆ / ብቸኝነት ዉስጥ ጠልቆ / ... በብቻ ዓለም ተንደላቆ” እያለ ለብቸኛ ህይወት ፌሽታ ተቀኝቷል:: የግጥሙ ርዕስ <አንዳንዴ> ነዉና ግለሰብ ቆይቶ ከሌሎች ጋር ተቀላቅሎ እንደ ወትሮው ህይወቱ በየእድሩ ትቀነጠባለች:: ሰዎች መካከል ሆኖ ብቸኝነት ከተሰማዉ ግን ጠነን ጐብደደ ይላል:: እዉስጡ በተጠነሰሰ ስጋት፣ ኩርፍያና ጥርጣሬ ከጀማዉ ባለመግጠሙ ባይተዋርነት እንደ ታማኝ ዉሻ ይከተለዋል:: መሬት ቢንቀጠቀጥ ዐይነስዉር ወዴት እንደሚሮጥ አያሳስበዉም:: ሳንወለድ የተቀባነዉ የህይወት ቅድመ ትርጓሜ የለምና ሳርተር እንዳለዉ <ሌላዉ ሰዉ ነዉ ገሃነም > በመሰለ የህልዉናነት ጭንቀት - existential anguish - የተሸበለለ ብቸኛም አለ:: ከዮፍታሄ “አይኔን ሰዉ አማረዉ ...” ጀምሮ ስለብቸኝነት የአማርኛ ገጣሚያን ተቀኝተዋል:: ሎሬት ፀጋዬ “ለየብቻዉ በመገንጠል // ተደባብቆ ሲብሰለሰል / ጉድም አይደል ? ድንቅም አይደል ?” እያለ ለብቸኞች - ለፍቅር ጦስ የተንገበገበዉ ያክል ባይጠልቅም - ተቀኝቷል:: [ እሳት ወይ አበባ ፥ 191] በዕዉቀቱ ስዩም በ<የባይተዋር ገድል> ያለአጋር ለቀረ ግለሰብ ዘምሯል:: “በሌሊት ወፍ ምትክ፣ ክንፍ ያወጣ ሌሊት፣ ጐጆህን ሲዞረዉ // መንሳፈፍ ይቅር፣ መስጠም ያቅተዋል ሰዉ ? / ሲያሰኝህ ዕድልህ / ያኔ ይጀምራል፣ የባይተዋር ገድልህ” ራስን እስከማጥፋት እንደ ደነበረ በሬ የሚያሯሩጥ፣ የሚገፈትር ብቸኝነት አለ:: [ ስብስብ ግጥሞች ፥ 72 ] እነሰለሞን ደሬሳ፣ ደበበ ሰይፉ... ተቀኝተዋል:: ብሩክ ገ/መድህን ይህን ለብቻ የመኮራመትን ሰቆቃ በ<ያኔ ነዉ ብቻ> ግጥሙ ተደምሞበታል:: “እንደምድረበዳ ቁልቋል፣ ብቸኝነት ሲገጥ / ከሰዉ በታች ዉሎ እያማጠ ሲያጥጥ / ያኔ ነዉ ብቻ / ሚታጣለት አቻ” [ ድርድር ፥ 19 ] በብዙ የፅሁፍና የቃል ግጥም የተገበረለት ብቸኝነት ምን ቢተርፈዉ ነዉ ነቢይ በተራዉ የተቀኘለት ?
የነቢይ ግጥም <ብቸኝነት የተደሰተበት ቀን> በምኑ ከሌሎች ተለየ ? ነቢይ ካሜራዉን ተሸክሞ ነዉ ብቸኛዉን ፍለጋ በየጉራንጉሩ የሮጠዉ:: እንደሌላዉ ለማተት፣ ያዉጠነጠነዉን ለመፍተል ብቻ ሳይሆን ባይተዋር ሲንቀሳቀስ እንዲጤንና አንባቢ ያሻዉን እንዲያክልበት በአንደምታ የተወረረ ግጥም ተቀኝቷል:: ግጥሙ የሚጀምረዉ ግማሽ በተረፈ፣ በተነካካ ቡናና ሲጋራ ነዉ:: የሚያምር ሳይሆን የቆሸሸ ጠረጴዛ ታክኮ፣ ከቁሳቁስ ጋር <ጉስቁልቁል ያለ ሰዉዬ> ተደባልቆ ተቀረፀ:: ካሜራዉ ሽፋኑን ሳይሆን የግለሰቡን ዉስጣዊ ሰቆቃ ለመግለብ አደፈጠ:: የግጥሙ አቀራረፅ በግዑዝ ቁስ እና በህይወት ንዝረት ይዋልላል፤ በሚዳበስና በማይዳበሰዉ:: ሲቋጭ ግን ዕልልታ የጋረደዉ ለቅሶና የመፈራረስ ድል የመሰለ አያዎነት ተጨናንቀዉበታል:: የብቸኛዉ ሰዉ እንቅስቃሴ ለመዉደቅ ነዉ ወይስ ለአዲስ ጉዞ መንገዳገድ ነዉ የሚለዉ አሻሚነት እንዳለ ሆኖ:: የግጥሙ አንጓ አቀራረፅ ያልተለመደ ነዉ:: አንድ ሀረግ “ቆየ ቆየና ግና፣” ሙሉ አንጓን ወክሎ የብቸኛዉ ጠባብ ተስፋ “ቡና የደረቀባት ማንኪያ” የመሰለ ሀቅ ይፈናጠርበታል:: የተናጋሪዉ ድምፀት ከገለልተኛ ወደ ተቆርቋሪ ብሎም የተደናገረ ደስታና ዕሪታ ዝብርቅርቅነት የዋጠዉ ልክ እንደ ብቸኛዉ ነፍስ ተርበትብቷል:: የአንጓዉ ክፍተት ዝም፣ ቀጥ ማለትን ይጠይቃል - መገጣጠምን የተጋፉ ስንኞች:: ነቢይ በዚህና በተነበበዉ < ነገሩ ገብቶኛል > ግጥም እንደተስተዋለዉ ለኪነዉበት የመዘርዘር ቅንያዊነት ይጠቀማል:: ማለትም እየመረጠ አልጋን እንደ መፅሄት ሲገላለጥ፣ ከባይተዋሩ ጠረጴዛ እንደ ካርታ እየሳበ ጆከሩን ሲያፈላልግ ይወስድ ይወስድና ከሆነ ሥነልቦናዊ አልያም ህይወታዊ ግድግዳ ያላትማል - ክህደትና ብቸኝነት የሚያካክል::
የሆነ ብሶት አለ:: መቆዘሙ፣ አካባቢዉን መዘንጋቱ፣ ጀማምሮ መተዉ፣ ጉስቁልናዉና እዉስጡ የሚፈላ ኑሯዊ ሀዘን፣ እጦት የመሰለ በሌላዉ አለመጤን፣ ችላ መባልም አለ:: ነፍሱ ዉስጥ የሰመጠ ሀዘን፣ የሚያደናግር ትዝታን የመሰለ፣ ከዕድሜዉ የረገፉ ብኩን ቀናትን ማስታወስ አይነት የመሸገበት እንቅስቃሴ አለ - ገጣሚዉ ሊያወረዛዉ፣ ሊያለሳልሰዉ ቢሞክርም:: ልክ ሰዐሊ መስፍን ሀብተማርያም በነፃ ግጥሙ እንዳወሳሰበዉ “የሚስጥሬን አበባዎች ዝምታዬ ዉስጥ ቀበርኳቸዉ /በስለዉም ሀዘን ሆኑ” መጐዳት አልያም ለከበባ እጅ አለመስጠት የመሰለ ህይወት:: በአካባቢያችን ለምደናቸዉ ልብ ባንልም ነቢይ የተቀኘለት በብቸኝነት የተተበተበ ይኖራል:: አለማየሁ ገላጋይ በ<ኩርቢቷ> አጭር ልቦለዱ ሰዎች መካከል ሆና ብቸኝነት የቆረፈዳት ወጣት እናት ስሏል:: ድንገት የሞተዉ ባሏ ቤቱንና ንብረቱን በእናት አባቱ ስም ስላስመዘገበ ለወለደችለት ልጅ ብላ ሁሉን ነገር ተነፍጋ፣ ተቸግራ ዝምታን ለምዳ አለማምዳም እንደጥላ ያለኮሽታ ትንቀሳቀሳለች:: ህፃን ልጇም ታዘበቻት <እዚህ አያቶቼ ግቢ ዉስጥ የኖረችዉ በመንፈስ ህልዉና ነዉ ማለት እችላለሁ:: ስትሄድ ኮቴዋ አይሰማም:: ለዚህ ዓለም ሙቀትና ቅዝቃዜ ምንም አይነት ምላሽ ስትሰጥ አይታይም:: አትስቅም፣ አታለቅስም:: ሆዷ ተከፍቶ ስትበላና ስትጠጣ አጋጥሞኝ አያዉቅም::> [ኩርቢት ፥ 53] ብቸኝነት የመጠጣት እናት አንድ ጠዋት ብድግ ብላ ጠፋች:: ነቢይ በዕምቅ አጭር ግጥም ዉጭና ዉስጥ እያጤነ የተቀኘለት ገፀባህርይ ሲንቀሳቀስ የአንድምታ ጨረሮች አፈነገጡ:: “ከነሃሳቡ / ከነሰባራ ኮከቡ” የቆዘመዉ፣ ልብሱ ብቻ ሳይሆን “ኑሮ እንደሸሚዝ ያለቀበት” ብድግ አለ:: የማጋትን ሲጋራ እግሩ ስር አልጣላትም፤ ከምሬት ጋር ወረወራት እንጂ:: እወረወረበት ድረስ ሄዶ ባለቀ ጫማዉ ወለሉ ላይ ደፈጠጣት:: ይህ ለምን አስፈለገ፣ ድርጊቱስ ምንን ይጦቅማል ?
በትርፍራፊ የተከበበዉ፣ የቀናቱ ኮከቡ የተሰበረዉና ዉጫዊ መልኩ አለባበሱ የተንገላታ፣ ምን በመሰለ አሳብ ነዉ የተዘፈዘፈዉ ? እንደቸገረዉ፣ ቁሳዊ ህይወቱ እንደጐደለዉ ያስታዉቃል:: ግን ከጀማዉ አግልሎ ያስቆዘመዉ አልተገለጠም:: መንቀሳቀስ ሲጀምርና
ሲጋራዉን ሲደፈጥጥ “አጅሬ ብቸኝነትም፣ ጮቤ ረገጠ ከልቡ ፍንድቅድቅ አለ በሀሴት / ባደባባይ ግዳይ ጣለ፣ አ.ን.. ድ ጠላት ወደቀለት !” ይህ ብቸኛ ግለሰብ < አ.ን.. ድ> የሚለዉ ቃል እንደ ሸክላ ከሶስት ቦታ ስለተሰነጠቀበት መፍረሱን አደመቀዉ:: ጭራሽ ራሱን አለመሳቱ፣ በቡና በሲጋራ መጠመዱ እንደመዘናጋት ስለሆነ ብቸኝነት ጮቤ የረገጠዉ ከነዚህ ጥቃቅን የእስትንፋስ ምልክቶች ብቸኛዉ የተላቀቀ መስሎት ነዉ:: ሆኖም የእንቅስቃሴዉ ጥንካሬ፣ ምሬቱ የመንገዳገድ ብሎም የማገገም፣ ከጉዳቱ የማሸለት ተስፋም ነዉ:: ነቢይ ቀቢፀ ተስፋነትን በግጥሞቹ አያባብልም:: ይህን የመሰለ ጨለማነት <ላምባዲናም የለኝ... > በሚለዉ ግጥም ከትንሽ ፍንጣቂ፣ ከሴት የፈገግታ ብልጭታ ተስፋ አያጣም:: “የሰባራ ኑሮ ሰባራ ኮከብም፣ ሙሉ ዕድሏ በርቶ / በጥርሷ ብርሃን፣ ብርሃን ተወልዶ፣ ብርሃን አፍርቶ” እያለ ነዉ ማንሰራራት እንደሚቻል፣ ጨለማ እንደሚረታ የተቀኘዉ:: ዕዉቋ ባለቅኔ Anne Sexton < ግጥም ህዋሳትን ማሸበር አለበት፤ የአንባቢን ስሜት እስከ ማደፍረስ> ላለችዉ ይህ ግጥም ወካይ ነዉ:: ተነቦ አይዘነጋም፤ ይኮሰኩሳል::

፬ ከሞት ጋር ተቃጥረን [ ስዉር-ስፌት ፥ 114]
ከሞት ጋር ተቃጥረን፣ የቆራጥ ቀጠሮ
ካምናም ብሶበታል ዘገየ ዘንድሮ::
ወትሮም እንዲህ ነዉ የአበሻ ቀጠሮ !!

ሞት ለካ አበሻ ነዉ ?!
ግና ምን ሆኖ ነዉ ?
እንዴት ቢንቀኝ ነዉ ?
እንዴት ቢፈራኝ ነዉ ?
መንገዱ ረዘመ ወይ መንገዱ ጠፋዉ ?
የህይወትን አጥር፣ ዳር ዳሩን ይዞራል !
ዕድሜን ደጅ ይጠናል::

ሞትም እንደሰዉ ልጅ ቀን ይጐድልበታል ?
በለስ የቀናት ለት
ህይወት እንደዚህ ናት
ሞትን መገነዣ፣ ስዉር ስፌት አላት !!
ሞትን መቅጠር፣ ለምንስ ቀረ ብሎ መብሰክሰክ መነሻዉ ምንድነዉ ? በኮሽታ የምትበረግግ ነፍስ የቤተክህነት እንጂ የመቃብር መረዋ አያረጋጋትም:: ስለ ድኅረሞት ህይወት የተሰበከዉ፣ ለመንደራችን የቋጠርነዉን ፍቅር ሊያስጥለን እንደማይችል ስብሀት በአጭር ልቦለዱ ቀርጾታል:: አጋፋሪ እንደሻዉ ከሞት ለማፈትለክ ሲባዝኑ አቡነ ተክለሃይማኖት <ወደ ሰማይ ቤት ልዉሰድህ> ቢሉት እንደ ቃርሚያ ቆጥራችሁ ናቁኝ በማለት አዲሳባ መመለስን ይመርጣሉ:: የመኖር ጣዕም እንዲሉ:: ሰዉ እድሜዉን ጨርሶ ከነምርኩዙ እመቃብር አፋፍ ቢደርስ ፣አፈሩን ገለባ እንዲያደርግለት እንሸኘዋለን:: ገና አቅምና ዕድሜ ተርፎት ድንገት በሞት ሲነጠቅ እንሸማቀቃለን:: በተለይም ዓላማ አንግቦ ለተበደሉት የሚተጋ ከሆነ:: አንድ ለህዝብ ጥሪ ዱር የገባ ጀግና ፣ የወሎ ሰዉ በድብቅ እየቀለበዉ ፣ ጐህ እንዲቀድ አብረዉት ህልም ይፈትሉ ነበር:: ረሀብ ገብቶ ትንሽ ትልቁን ፈጀዉ:: ህዝብ እጅ አጠረዉ፤ ጀግናዉም ብሩክ ጠኔ ገደለዉ:: ቅኔ አዋቂ “ብሩኬ ሞተ አሉ ቋጥኝ ተጭኖበት / ገደሉን ሲቧጥጥ አገልግል ጠፍቶበት” በማለት የማይዳሰስ ሀዉልት አዋቀረለት፤ ለሌላ ፋኖ አሻገረዉ:: ታድያ ነቢይ እንደ ተቀኘዉ ምን ሲኮን ነው ሞትን ቀጠሮ አክብረን የምንጠብቀዉ ? ሞትን በጉጉት መጠበቅ በዝቶ መሽቀዳደምም አለ:: <የሰዉ ህይወት፥ በበረሃ ዉስጥ ሲጓዝ ዉሃ የጠማዉ ሰዉ፥ ራቅ ብሎ ከወደፊቱ ኩሬ እንደሚታየዉ ዐይነት፥ የቀን ቅዠት ነዉ ... በበኩሌ ከመሆን አለመሆንን እመርጣለሁ:: > [አንድ ለአምስት ፥ 303] አስፋዉ ዳምጤ የገለፁት የሥነልቦና ምሁር ወንድይራድ ልጥ ልጦ ገምዶ በአፍላ ዕድሜዉ ዛፍ ላይ የገዛ ህይወቱን አሳለፈ:: አንባቢ ስለ ግል ህይወቱ ለማዉጠንጠን ይገደዳል:: ነቢይ ለበዐሉ ግርማ ባበረከተዉ ግጥም

ይሄ ምን አማርኛ ነዉ፣ ፌዙ ለጆሮ የከፋ
ምን ያለስ ልብስ ሰፊ ነዉ፣ ሞትን በልኬ እሚሰፋ ?
ሞት ከአረጋዊ ቢያረጅም፣ ከሰዉ የባሰ ክፉ ነዉ
በተለይ ደራሲ ሲያገኝ፣ ሲስገበገብ ለብቻዉ ነዉ > በማለት ተመስጧል::
ሞት እርጅና አድፋፍሮት ከሰዉ ጋር ብርድ ልብስ ቢናጠቅ አያስደንቅም:: ዕድሜ እየፈራረሰ አጥንት ከረገበ፣ ህልዉና ከቀረፈፈ ማንን ይለማመጣሉ ? የመኖር ሸክም የሰበረዉ ወይም አንዳች ህልዉናዊ ጭንቀት የቀፈደደዉ ሞትን ይመኛል:: ለዚህ እንግልት በሥነቃል የተዘረፈ ቅኔ አለ “ሞት ይቅር ይላሉ ቢቀር አልወድም / ድንጋዩም አፍሩም ከሰዉ ፊት አይከብድም” ተብሏል:: የደበበ ሰይፉ ግጥም <ለምን ሞተ ቢሉ> ይታወሳል:: ነቢይ ግን “መንገዱ ረዘመ ወይ፣ መንገዱ ጠፋዉ ?” ሲል ዘመቻ ሄዶ ያልተመለሰን አባወራ ነቅቶ የመጠበቅ ጉጉት ቢመስልም ነፍስ ገዳይ በመዘግየቱ መታወክን ምን ቀሰቀሰዉ ? በአንፃሩ ደግሞ እንደ አጋፋሪ እየጋለበ ከሞት የሚሸሸ አለ:: መሸሸ ሳይበቃ፣ አፈታሪክ ተዋናይ የሚባል አዋቂ ሞትን ለሰባት አመት መገደቡን ያወጋል:: ተዋናይ በጐጃም የነበረ ፈላስፋ፣ ታላቅ ሊቅ፣ ቅኔን የፈጠረ ባህረ ምስጢሩን ዋኝቶ የመረመረ መሆኑን ተነግሮለታል:: በዕዉቀቱ ስዩም ለሰባት አመት ተዋናይ ሞትን መገዘቱ ርዑየትን በመፃረሩ ይበልጥ ለጐደጐደዉ ህልም አደላ:: “ተዋናይ ስለምን እግዜርን ይከሳል / ሞት አንዴ ይመጣል! ሕልም ይመላለሳል / መቃብርን ደፍኖ ሞትን በቁም አስሮ / ሰዉ ነፍሱን ይቀብራል ? ሕልሞቹን ቆፍሮ” [ስብስብ ግጥሞች ፥ 103] ነቢይ <ከሞት ጋር ተቃጥረን> ግጥሙን ያበረከተዉ - ለፍትጉና ለህቡዐን ህይወት - ነዉ:: አብርክቶቱ ዳር የተረሳ ትራፊ ሳይሆን የሚነዝር ምስጢር የቆጠበ ስንኝ ነዉ:: ፍትጉ ድሮ በጐህ መፅሄት ይሳተፍ የነበረ - ምናልባትም የብዕር ስም - ሲሆን፣ ህቡዐን ህይወት ለመራራ ህዝባዊ ትግል፣ ለአላማ ህይወቱን ለመማገድ ላላቅማማዉ ንቁ ወጣት ጥቆማ ነዉ:: ይህ ጥቆማ የሞትን አዉድና እሴት አበለፀገ::
ግጥሙ ሲዋቀር ሶስትዮሽ አዝሎ ነዉ:: ከሞት ጋር ቆራጥ ቀጠሮ፥ ሞት ዕድሜን ደጅ መጥናቱ እና ህይወት በለስ ሲቀናት :: የተናጋሪዉ ድምፀት በህይወት ሳይሆን በሞት ላይ መቀለድን መዝናናትን፣ የአበሻ ቀጠሮ ይመስል ለጊዜ ቁብ መንፈግን ታክኮ አይደብትም:: በጥልቀት ሲጤን ህይወት ሞትን ድል የሚነሳት ዝም ብሎ በመኖር አይደለም:: ተራ ሰዎች ተስፋና ደስታ እንዳይነፈጉ ስንዳክር፣ በጥሞና ሲመሽና ሲነጋ ብቻ ነዉ:: ነቢይ በሌላ ግጥሙ እንዳለዉ “በጥላ በጣዩ ረክቶ በጥሞና ለሚኖረዉ / እያንዳንዱ ማታና ቀን፣ የራሱ ዘላለም ነዉ” ይህን ዘላለም ከአንድ ዕለት መዝምዞ ለመታደስ ወኔ ይጠይቃል:: እያንዳንዷን ቀን ለተንገላቱት በመላተም እንደሚቆላ ተልባ፣ ብርሃን ከደሳሳ ጐጆ ማፈናጠር፣ በዕንባ የረጠቡ አይኖች ስቀዉ ደስታቸዉ ሲጋባብን ለነሱ ድል “ሞትም እንደሰዉ ልጅ ቀን ይጐድልበታል ?” እየተባለ ያጣድፋል:: ሀዲስ ዓለማየሁ የገለፁት በዛብህ፣ የስዕለት ልጅ ስለሆነ የእናቱን ቃልኪዳን አክብሮ ታቦት ለማገልገል ማፈግፈግ አለበት:: በዛብህ አይነ ጥላዉ ተገልጦ እንደ ነፃ ሰዉ መኖር ቢያልምም፣ የእናትና አባት ፍላጐት ከማመፅ አገደዉ:: <በመሄድና በመመለስ አዉታር ተወጥሮ> በደመ ነፍሱ ሞታቸዉን ሳይመኝ አልቀረም:: የሁለቱንም ሞት ካረዱት በኋላ እንደምንም አለቃቅሶ <... ቀለለዉ፤ ... ደስ አለዉ:: ... ወደሁዋላ የሚጐትተዉ ነገር ሣይኖር ... የፈለገዉን አይነት ህይወት መኖር ይችላል ... ወቃሽ ከሳሽ ሳይፈራ> [ ፍቅር እስከ መቃብር ፥ 63 ] በሌላዉ ሞት ምክንያት ህይወቱ ነፃ ወጣች:: ይህን ለመሰለ የሞት ቀጠሮ “ካምናም ብሶበታል ዘገየ ዘንድሮ” እያለ የሌላዉን ሞት እንደ በዛብህ ለሚቋምጥ አይደለም ነቢይ የተቀኘዉ:: የበዛብህ እንደ ተረት ነዉ፤ ለራስ ጉዳይ በትንሹ በትንሹ መሸራረፍ:: ነብይ ገዋ ሰዉ የሚለዉ አይነት “ብዙ ሰዉ ባለበት አገር፣ ብዙ ባዶ ይታየኛል”:: ይህን ብርቅ ህይወት ለተጐዱት አርነት መማገድ፣ ራስንና ዕድሜን አሳልፎ መስጠት፣ ለወሰነ ጀግና ነዉ የተቀኘዉ:: በድሉ ዋቅጅራ ከደብረ ማርቆስ እስር ቤት በቀይ ሽብር ሊገደል ስሙ ስለተጠራ “ከእሱ በቀር / ያቺን የህይወትና ሞት ድንበር” ማንም ለማይጋራዉ ወጣት እንደ ዘመረዉ አይነት:: [ፍካት ናፋቂዎች ፥ 63 ]
<ከሞት ጋር ተቃጥረን> ለቀዘዘ ህይወት ሳይሆን ሌሎችን ከእንግልት ለማስጣል መስዋዕት ለሚጠይቅ ኅላዌ ነዉ የተገጠመዉ:: <እስረኛዋና የሰጠመችዉ ፀሐይ > ገፅ 137፣ <እስርቤትና ጊዜ > ገፅ 138፣ ግጥሞች የክትና የአዘቦት ህይወትና ሞት ይደፍቃሉ:: ቀጠሮ አክብሮ ይመጣል የተባለዉ ሞት “የህይወትን አጥር፣ ዳር ዳሩን ይዞራል ! / ዕድሜን ደጅ ይጠናል::” ተብሎ እስኪናቅ ድረስ ተሰለቀበት:: ሆኖም ለህዝብ ጥሪ ሳያቅማማ ያመፀዉ፣ አያሌ ፈተናን አሸንፎ እንደ ትዝብት የተናደዉን ትናንት ሲያጤን፣ አሁንም በመተንፈሱ ለኑሮ ረቂቅ ፍቅር ያጥወለዉለዋል:: “በለስ የቀናት ለት / ህይወት እንደዚህ ናት / ሞትን መገነዣ፣ ስዉር ስፌት አላት !!” ነቢይ ለግጥሞቹ ስብስብ የመረጠዉ ርዕስ
(ስዉር-ስፌት) በዚህ ግጥም መዉጫ፣ ከግማሽ ስንኝ ዉስጥ የተወሸቀ ዕንቁ ነዉ - እንደ ሽንኩርት ተልጦ የማያልቅ:: ስለ ህይወትና ሞት የዕድሜና የገጠመኝ ጨመቅ ማጠንፈፍ በቂ ነዉ::

ጊዜ እንደ ፀጥታኮ ነዉ፣ ላፍታ አይታሰርም ከቶ
ሰዉ እንኳንስ ጊዜን ሊያስር፣ ሊኖር ጊዜ የት አግኝቶ
በማለት ነቢይ የጊዜ አሸናፊነትና የእስር ቤት መናድን አብስሯል:: ማንንም ከማታዉቅበት ከተማ ብትኖር፣ በርህ በተደጋጋሚ ሲንኳኳ ተነስተህ ለመክፈት ፍላጐት ከሌለህ ? ከፈራረሰ ጐጆ የሚያገለግል መስኮት ከተረፈህ በቂ ነዉ ወይ ? በየህይወትህ ምዕራፍ የምትዳብሰዉ ስዉር-ስፌት ዘወትር ያስፈልግሃል::
ይቀጥላል

Published in ጥበብ

በ2013 የካሬብያን የፋሽን ሳምንት በኢትዮጵያዊቷ ዲዛይነር ፍቅርተ አዲስ የቀረቡ ዘመናዊ ፋሽን ያላቸው የአገር ባህል አልባሳት ተደነቁ፡፡ ዲዛይነር ፍቅርተ ባህሏን መሰረት አድርጋ እጅግ ውብና በየትኛውም ወቅት ሊለበሱ የሚችሉ አልባሳትን የፋሽን ዲዛይኖችን በማቅረብ ዘመን የማይሽራት ሴት መሆኗን አስመስክራለች በሚል “ዘ ጃማይካ ኦብዘርቨር” አድንቋታል፡፡ መቶ በመቶ በኢትዮጵያ በበቀለ ጥጥና ፈትል የተሰሩት የፍቅርተ የአገር ባህል አልባሳት በፋሽን ሳምንቱ ልዩ ትኩረት እንዳገኙም ዘገባው ጨምሮ ገልጿል፡፡ የፍቅርተ አዲስ የፋሽን ዲዛይኖች በካሬቢያን የፋሽን ሳምንት የአፍሪካ አልባሳት ላገኙት ተቀባይነት አስተዋፅኦ ማድረጋቸውን የገለፀው ደግሞ ሌላው የጃማይካ ጋዜጣ “ዘግሊነር” ነው፡፡ የፋሽን ሳምንቱ ባለፈው ሳምንት በጃማይካዋ ከተማ ኪንግስተን የተካሄደ ሲሆን ከመላው ካረቤያን፤ ከመካከለኛው አሜሪካ፤ከሰሜን አሜሪካ፤ ከዚምባቡዌ እና ከኢትዮጵያ የተወከሉ ታዋቂ ዲዛይነሮች ተሳታፊ ነበሩ፡፡

ከዲዛይነሯ ፍቅርተ አዲስ ጋር ሌላዋ ኢትዮጵያዊት ማፊም አልባሳቷን እንዳቀረበች ያመለከቱት ዘገባዎቹ አልባሳቶቻቸው በቆንጆዋ ሱፕር ሞዴል ዮርዳኖስ ማራኪ አቀራረብ ታዳሚውን እንደማረኩ ገልፀዋል፡፡ በ2009 እኤአ ከላይ ‹የፍቅር› በሚል መጠርያ የራሷን የፋሽን ብራንድ የመሰረተችው ወጣቷ ዲዛይነር ፍቅርተ ላለፉት ሶስት አመታት በአዲስ አበባ በተካሄደው ሃብ ኦፍ አፍሪካ ፋሽን ዊክ ከመሳተፏም በላይ አምና እና ካችአምና በኒውዮርክ ከተማ በተደረገው አፍሪካ ፋሽን ዊክም የፋሽን ስራዎቿን አቅርባለች፡፡ ፍቅርተ የፋሽን ዲዛይን ፍላጎት ያደረባት የሁለተኛ ደረጃ ተማሪ በነበረችበት ጊዜ ሲሆን ሙያው ለፈጠራ በሚሰጠው ነፃነት ሁልጊዜም ደስተኛ እንደሆነች ተናግራለች፡፡

ኢትዮጵያዊ ባህልን መሰረት በማድረግ የፋሽን ውጤቶቿን በዓለም የፋሽን መድረክ ተወዳዳሪ የማድረግ አላማ እንዳላት በኦፊሴላዊ ድረገጿ አስታውቃለች፡፡ ‹የፍቅር› በመባል የሚታወቁት የፍቅርተ የልብስ ፋሽኖች በማንኛውም ወቅት መለበስ የሚችሉ፤ ዘመናዊነት እና ባህላዊነትን ያጣመሩ እና ተፈጥሯዊ መስህብ እንዳላቸው ተመስክሮላቸዋል፡፡ በዴቨሎፕመንት ሳይኮሎጂ ሁለተኛ ዲግሪ ያላት ፍቅርተ፣ የህፃናት ስነልቦና አማካሪ ሆና ብትሰራም አሁን የፋሽን ዲዛይን ሙያ የሙሉ ጊዜ ስራዋ ሆኗል፡፡

ዘ ሮክ ዘንድሮ በተወነባቸው ፊልሞች ከ1.5 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ በማስገኘት የሚስተካከለው አለመገኘቱን ቢዝነስ ኢንሳይደር ዘገበ፡፡ ፕሮፌሽናል የነፃ ትግል ስፖርተኛ የሆነውና በሙሉ ስሙ ድዋይን ጆንሰን ተብሎ የሚታወቀው ዘ ሮክ፣ ላለፉት 16 ሳምንታት በቦክስ ኦፊስ የገቢ ደረጃ ከአንድ እስከ 10 ባለው ቦታ ባለመጥፋት ስኬታማነቱን አረጋግጧል፡፡ በ2013 ለእይታ የበቁት ዘ ሮክ የተወነባቸው ፊልሞች ‹ስኒች›፤ ‹ጂ.አይ. ጆ ሪታልዬሽን›፤ ‹ፔይን ኤንድ ጌይን› እና ሰሞኑን መታየት የጀመረው ‹ፋስት ኤንድ ፊርዬስ 6› ናቸው፡፡ በገቢ በጣም ስኬታማ የሆነባቸው ሁለቱ ፊልሞች በመላው ዓለም 365.53 ሚሊዮን ዶላር ያስገባው ‹ጂ.አይ. ጆ ሪታልዬሽን› እና 586.66 ሚሊዮን ዶላር ያስገኘው ‹ፋስት ኤንድ ፊርዬስ 6› ይጠቀሳሉ፡፡ በተወነባቸው ፊልሞች ገበያው ለምን እንደተሟሟቀለት የተጠየቀው ተዋናዩ በሰጠው ምላሽ ባለፉት 13 ዓመታት በትዋናው በመስራት ከፍተኛ ጥረት እና ትጋት እንደነበረው ገልፆ “ከፍተኛ ስኬት የማስመዝገብ ግብ ነበረኝ” ሲል ተናግሯል፡፡

ታዋቂው የፊልም ዲያሬክተር ጄ ጄ አብርሃምስ በ‹‹ስታር ትሬክ ኢንቱ ዳርክነስ›› ፊልም ባገኘው የገቢ ስኬት የጆርጅ ሉካስ ፊልም የነበረውን ስታርዋርስ 7ኛ ክፍል እንዲሰራ መዋዋሉን ዋሽንግተን ታይምስ ዘገበ፡፡ በጂን ሮደንበሪ በተደረሰው የስታር ትሬክ መፅሃፍ ላይ ተመስርቶ የተሰራውና የስታር ትሬክ የተሰኘ ፊልሞች ፍራንቻይዝ 12ኛ ክፍል የሆነው ‹‹ስታር ትሬክ ኢንቱ ዳርክነስ›› በመላው ዓለም ያስገባው ገቢ 376.54 ሚሊዮን ዶላር ደርሷል፡፡ የስታር ትሬክ ፊልሞች ፍራንቻይዝ መሰራት ከጀመሩ 38ኛውን ዓመት ሲሆናቸው፣ ዘንድሮ ለእይታ የበቃውን 12ኛውን ክፍል ጨምሮ ያስገኙት ገቢ ከ1.628 ቢሊዮን ዶላር በላይ ነው፡፡

‹‹ስታር ትሬክ ኢንቱ ዳርክነስ›› በ190 ሚሊዮን ዶላር በጀት የተሰራና በፓርማውንት ፒክቸርስ የሚከፋፈል ሳይንሳዊ ልቦለድ ፊልም ነው፡፡ ፊልሙ በምድር አቅራቢያ ስለምትገኝና ጥንታዊ የዩኒቨርስ ስልጣኔ ያላት የኒብሩ ፕላኔት ፍጡራን በሰው ልጆች ላይ ስለሰነዘሩት የሽብር ጥቃት የሚተርክ ነው፡፡ ዲያሬክተር ጄጄ አብርሃምስ በ‹‹ስታር ትሬክ ኢንቱ ዳርክነስ›› ያገኘው ስኬት ነው የስታር ዋርስ ፊልሞች 7ኛ ክፍልን እንዲሰራና የገቢ ስኬቱን እንዲቀጥል ተመራጭ ያደረገው፡፡ የስታር ዋርስ 7ኛ ክፍል ቀረፃውንም በ2014 እንደሚጀምር ተገልጿል፡፡ የስታር ዋር ፊልሞች ፍራንቻይዝ በእውቁ ዲያሬክተር ጆርጅ ሉካስ የተሰሩ ሲሆን በመላው ዓለም ከ1.85 ቢሊዮን ዶላር በላይ አስገኝተዋል፡፡

የሠአሊ አዳምሰገድ ሚካኤል የሥእል አውደርእይ ከትናንት በስቲያ ተከፈተ፡፡ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም የተከፈተው አውደርእይ እስከ መጪው ረቡዕ ለሕዝብ ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡

በምስጋና አጥናፉ ተጽፎ ዳይሬክት የተደረገውና በፓስፊክ ፊልም ፕሮዳክሽን የተዘጋጀው “ጥቁር እና ነጭ” ፊልም የፊታችን ሰኞ በብሔራዊ ትያትር ከቀኑ በ11 ሰዓት ይመረቃል፡፡ በዚህ የቤተሰብ ፊልም ላይ ሙሉአለም ታደሰ፣ እመቤት ወልደገብርኤል፣ ማክዳ አፈወርቅ እና ሌሎችም ተውነዋል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኘው የሉሲ አካዳሚ ተማሪዎች በየክፍላቸው ንዑስ ቤተመፃሕፍት አቋቋሙ። የሕፃናትንና ታዳጊ ወጣቶችን የንባብ ባህል ለማዳበር የተቋቋሙትና ትላንት የተመረቁት የየክፍሉ አብያተ መጻሕፍት በዝነኛ ሰዎች ስም ተሰይመዋል። ከ1ኛ-5ኛ ክፍል ያሉ ተማሪዎች ያቋቋሙት ቤተመጻሕፍት በደራሲ ሜሪ ጃፋር ስም የተሰየመ ሲሆን ቤተመጻሕፍቱን ደራሲ ሜሪ ጃፋር መርቀውታል፡፡ በክቡር ዶ/ር ከበደ ሚካኤል የተሰየመውን የ7ኛ ክፍል ቤተመፃህፍት ደግሞ ኢንጂነር ታደለ ብጡል ሲመርቁት በደራሲና ጋዜጠኛ ስብሃት ገብረእግዚአብሔር የተሰየመውን የ11ኛ ክፍል ቤተመፃህፍት ጋዜጠኛና ደራሲ ዘነበ ወላ መርቀውታል። ለ12ኛ ክፍል የሚያገለግሉት ሁለት አብያተ መጻሕፍት በክብርት ዶ/ር ስንዱ ገብሩ እና በደራሲ ፀሐይ መላኩ፣ የተሰየሙ ሲሆን አምባሳደር ዶ/ር ሳሙኤል አሰፋና ደራሲ ፀሐይ መላኩ መርቀውታል፡፡ ትምሕርት ቤቱ ካሉት 18 መማርያ ክፍሎች ስድስቱ በዚህ መልኩ ቤተመጻሕፍት ያገኙ ሲሆን የሌሎችም እንደሚቀጥል ማወቅ ተችሏል፡፡

በጋዜጠኛ፣ ደራሲና ጸሐፌ ተውኔት ቴዎድሮስ ተክለአረጋይ የተዘጋጀው “ፍልስምና ፫” የተሰኘው መፅሃፍ ለንባብ በቃ፡፡ በቃለ ምልልስ መልክ በተዘጋጀው መጽሐፍ ውስጥ ስምንት ባለሙያዎች የተካተቱ ሲሆን ከእነዚህም መካከል ኬሚካል ኢንጂነር ጌታሁን ሄራሞ፣ በቀለማት ፍልስፍናና ሥነ ልቦናዊ ማንነታቸው፣ ተፊሪ ንጉሤ በገዳ ሥርአት፣ በዋቂፈናና ኢሬቻ፣ ዶ/ር መስፍን አርአያ በማንነታችን ላይ የተናገሩት ይገኝበታል፡፡ 144 ገፆች ያሉት መጽሐፍ በ32 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

በሌላ በኩል በግዛው ዘውዱ የተዘጋጀው “ኢትዮጵያ፣ ታሪክ፣ ትርክትና ታሪካችን” መጽሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ በ285 ገጾች የተቀነበበው መጽሐፍ በፋርኢስት ትሬዲንግ የታተመ ሲሆን በ60.70 ብር እየተሸጠ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ መጽሐፉ በማጣቀሻነት ከተጠቀማቸው በርካታ ዋቢዎች መካከል የአለቃ ደስታ ተክለወልድ፣ የፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ፣ የነጋድራስ ገብረሕይወት ባይከዳኝ፣ የአሌክሳንደር ቡላቶቪችና የዶናልድ ሌቪን መጻሕፍትና ሌሎች ጽሑፎች ይገኙበታል፡፡

በኢትዮጵያ የመጀመርያው የኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያ ኤፍኤም አዲስ 97.1 የተመሰረተበትን 13ኛ ዓመት በዓል ነገ ከጧቱ 3 ሰዓት ጀምሮ በሐራምቤ ሆቴል እንደሚያከብር አስታውቋል፡፡ የ24 ሰዓት ስርጭት ያለው ብቸኛው የኢትዮጵያ ሬዲዮ ጣቢያ፣ ነገ በሚያከብረው በዓል ላይ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር ረዳት ፕሮፌሰር ታደሰ ዝናዬ “የኤፍ ኤም ጣቢያዎቻችን ለሕብረተሰብ ሁለንተናዊ እድገትና ለሀገር ልማት ያበረከቱት አስተዋጽኦ እና ጉድለቶቻቸው” በሚል ርእስ እንዲሁም የጣቢያው ጋዜጠኛ አቶ ዮናስ ወልደየስ “ኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ከየት ወደየት?” በሚሉ ርእሶች ጥናታዊ የውይይት ፅሁፍ ያቀርባሉ፡፡ በውይይት ላይ ከ100 በላይ ተጋባዥ እንግዶች እንደሚገኙ የታወቀ ሲሆን ጣቢያው ከበዓሉ በኋላ የአንድ ዓመት ተኩል ጥናት ያደረገበትን የዝግጅቶች ለውጥ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

Saturday, 15 June 2013 11:18

ሕልምና ቅዠት

እሷ

ይኸ ሕይወትን በጅምላ የሚያስሮጠኝ ዕድሜ፣ ቀኔን እንደ ጉልት ሽንኩርት ሲቸርችረኝ ይውልና መኖሬን ሲያዝለው፣ የድካሜን ጣመን ልወጣ እተኛለሁ፡፡ እናም የተስፋዬን ምንጣፍ ነገዬን ዘርግቼ ተኛሁ፡፡ እንደተኛሁ ሰመመን ይመስል አንዴ ሲያሸልበኝ ወዲያው እየባነንኩ ጥቂት ከቆየሁ በኋላ ድካሜ በርትቶ ዕንቅልፌ ጭልጥ አድርጐ ወሰደኝ፡፡ እንደወሰደኝ በዕንቅልፌ መሀል እንዲህ ሆነ፡፡ ይመስለኛል ጭ...ል...ጥ ያለ ምድረ-በዳ ነው፡፡ ውኃ ሰው ጠምቶኛል፡፡ ነገር ግን ጥሜን የሚከላ ምንም ጠብታ የለም፡፡ በዚያ ንዳድ ብቻዬን እንደ ቆምኩ “የሰው ያለህ!” እያልኩ ሰው እፈልግ ጀመር። ዙሪያዬን እየቃኘሁ በጩኸት ብጣራም የራሴን ድምፅ ከመስማት በቀር አቤት የሚለኝ ጠፋ፡፡

“የሰው ያለህ!” እያልኩኝ በጩኸቴ ብደክምም ሰው ናፍቄ እንደተኛሁ ሰው ናፍቄ ባነንኩ። ከዕንቅልፌ እንደነቃሁ እሷን ከአጠገቤ አየኋት፡፡ እንዳየኋትም በህልሜ ያየሁትን ሁሉ እንድትፈታልኝ ነገርኳት፡፡ ከጐኗ እንደተቀመጥኩ የሕልሜን … ሕመሜን ሰምታኝ … ሰምታኝ ስታበቃ “ይህ ቅዠት ነው!” አለችኝ! … እኮ እንዴት? ውሎዬን ደክሜ ስንዝር ጋደም ባልኩኝ ቁጥር ሌቱን ሳታት እየቆምኩ የውኔን ልደገፈው ሰው መሆን ዳዊቴን ሳነበንብ ዝርው በተበተንኩ! … እውነትና ሰውን ስፈልግ እንደ ጀምበር ሽርትት ሳሽቆለቁል እያየች? በውን የናኘሁት ውሎ በሕልሜ እያጐነቆለ ነብሴን ሲያባክነው “ለእሷ ቅዠት የሆነባት ምኔ ብታየው ይሆን? ከመኖሬ ጉድጓድ ሸማ ተዘርግቼ ኩታ ዕድሜ ልሸምን በቀንና ለሊት መወርወሪያ መሀል ቀሰም ተጋድሜ እያየች … ቅዠት ነው? ሕልሜ እንደ ጥፍጥሬ ተፈልቅቆ፣ ይኸ ደጋን ኑሮዬ በቀን እየተነደፈ፣ ጥሜ እየተባዘተ ቀጭን ብፈተላት፣ ኑሮ ቅዠት ባልሆነባት ነበር! ውኃ ሰው ጥማቴን ሳትጠማ፣ ሀሩሬን ተቃጥላ ጩኸቴን ሳታዳምጥ፣ ሰው ተርባ የናፍቆትን ክሳት ሳትረዳ፣ የባይተዋርነትን ፍርሃት፤ የብቸኝነት መራራ ጣዕም ሳትቀምሰው እንዴት ህልሜን ታረክስዋለች … እብሰለስላለሁ፡፡ እየተብሰለሰልኩ እባክሽ ሆድዬ … ሕልሜን አታርክሺው እላታለሁ፡፡ በአንድ መንግሥታዊ ያልሆነ የዕርዳታ ድርጅት ውስጥ ሠራተኛ ነኝ፡፡

እንግሊዛዊቷ ክርስቲና፣ አሜሪካዊቷ ሊዛና ታይላንዳዊቷ ዚሃ የሥራ ባልደረቦቼ ናቸው፡፡ ከመስክ ሥራ ስንመለስ አክስቴ ያፈላችውን ቡና ሳይጠጡ ወደ ቤታቸው አይሄዱም፡፡ ዛሬም እንደተለመደው ቡናቸውን አጣጥመው ሸኝቻቸው መመለሴ ነው፡፡ የጠጣሁት ቡና ስላነቃቃኝ ከመተኛቴ በፊት ዜና ለመከታትል ቴሌቪዥኔን ከፈትኩ፡፡ እሱ እሱን ሳውቀው ሃያ ዓመታት አለፈ፡፡ ተስፋ ላጣች ወንበሩ ሽቅብ ቁልቁል እያለ ሲባዝን፣ ሥልጣን የሚሏት ጣር ፈተናዋ በዝቶ በእግሬ ቆምኩኝ ሲል ዘርጥጣ እየጣለች መነሻው ሲጠፋበት አየዋለሁ። ሽበቱ ገብስማው እስከሚታይ ድረስ ተስፋው እየሸሸበት፣ ግብሩ ዘመኑን በዜሮ እያባዛው ቀኑ ሲመሽበት አየዋለሁ፡፡

የቀናቶቹን ቀን ከተስፋ ባህር ላይ በተስፋ እየጨለፈ፣ የተስፋ አክርማውን በተስፋ እየቀጨ ምኞቱ ያደመቀውን ሙዳይ ሲሰፋ … ሲሰፋ … የሰፋው ሙዳይ ተስፋ ሳይቋጥር አንድ ጊዜ ከዚህ አንድ ጊዜ ከዚያ ተስፋ እየቆነጠረ … በግብረ አልቦ ሰማይ ላይ ምኞቱ የዘራውን ኮከብ ሲቆጥር … ሲቆጥር … ሃያ ዓመታት ሙሉ በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ እያለ አየዋለሁ፡፡ ያየሁት ለታ የልቡን ሳይሆን ያፉን ይነግረኛል፡፡ ከረባትና ሱፍ ቢቀያይርም ንግግሩ አርማ ስላለው አውቀዋለሁ፡፡ በማያልቀው ነገ … ነገ ይሳካል ይለናል … ለሞተበት ተስፋ ትንሣዔ እንድንሆነው ገንዞ ሳይቀብረን፣ በተባ አንደበቱ የለመድነውን ሞት ደጋግሞ ይገለናል፡፡ ዛሬም እንደ ትናንት የሰላ አንደበቱ ቢጐለድፍም ጭብጧችንን በተስፋ እየቀማ “እኔ ዛሬ ልብላው ለእናንተ ደግሞ ነገ” ይለናል፡፡ በተስፋው እየገደለን … በምላስ እያባባለን … ሲደልለን … ሲደልለን … ኡፍፍ … ደከመኝ፡፡

ቴሌቪዥኑን አጠፋሁትና ተኛሁ፡፡ እንደተኛሁ… በልማደኛው ህልሜ ውስጥ ያ ሃያ ዓመት ሙሉ በቴሌቪዥን መስኮት የማየውና አንድም ቀን አግኝቼው የማላውቀው ሰውዬ፤ ገብስማ ፀጉሩን እያከከ ከአጠገቤ ቆመና አንድ ወረቀት አቀበለኝ፡፡ “ምንድን ነው?” አልኩት “እ… እንደምታውቀው በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ሁኔታ ሙስና ላይ ዘመቻ እያካሄድን ነው …እ… እንደምታውቀው “የዓሣ ግማቱ ከጭንቅላቱ” እንደሚባለው ከጭንቅላቱ ጀምረናል፡፡ ወደታች ማጥራቱም ቀጥሏል … ስለዚህ በቦታው ክፍተት እንዳይፈጠር ምክትል ዳይሬክተር ሆነህ በጊዜያዊነት እንድትሰራ አንተን መርጠንሃል እ … በቦታው ክፍተት እንዳይፈጠር … ስለዚህ አሁን ሄደህ ሥራህን ጀምር አለኝ” እኔ ግን “የዓሣ ግማቱ ከጭንቅላቱ” የሚለውን አባባል እያስተነተንኩ ነበር፡፡ ቆይ … የዚች ሀገር ጭንቅላት ያለው ጉምሩክ ውስጥ ነው እንዴ?” አልኩኝ በልቤ፡፡ አፍ አውጥቼ ለመናገር አልደፈርኩም፡፡ አንድ ሰው ሲሾም ምን እንደሚሰማው ለማወቅ ፈልጌያለሁ፡፡ እናም ወደ ጉምሩክ ዋና መሥሪያ ቤት አመራሁና የምክትል ዳይሬክተሩን ቢሮ ከፍቼ ገባሁ፡፡

ጠረጴዛው ላይ ሻንጣዎች አሉ፡፡ ማን አስቀመጣቸው? … ለም አስቀመጣቸው? አንድ አዲስ ሰው ሲሾምና ቢሮውን ከፍቶ ሲገባ … ጠረጴዛው ላይ የሚጠብቀው ሻንጣዎች ነው? ተራ በተራ ከፈትኳቸው” አንዱ በዶላር ተሞልቷል! … በሚቀጥለው ዩሮ! … በሚቀጥለው … ፓውንድ! … ጥቂት የታይላንድ ገንዘቦች ጠረጴዛው ላይ ተበታትነዋል፡፡ ይኸ ሁሉ የኔ ቢሆንስ? … ልክ ይኸን እንደተመኘሁ አስራ አንድ በመቶ አይደለም! (በለው!) … አርባ አራት በመቶ ያደግን መሰለኝ! በሕልሜ መሀከል “እርጉዝ ላም ያለው ድርቅን አያውቅም” የሚለው ብሂል ቢመጣም ከልቤ አልጣፍኩትም፡፡ ብሮቹን ተራ በተራ በእጆቼ መዳሰስ ጀመርኩ፡፡ መዳሰስ ብቻ! ወይ አንስቼ አልጨበጥኳቸው ወይ ወደ ኪሴ አልከተትኳቸው እንዲሁ እየዳሰስኳቸው ሳለ ከዕንቅልፌ ነቃሁ፡፡ እንደ ነቃሁ ዙሪያዬን ተመለከትኩ፡፡ ማንም ካጠገቤ አልነበረም፡፡

“ድኃ በህልሙ ቅቤ ባይጠጣ ንጣት በገደለው ነበር!” ሳቄን ለቀቅሁት! እየሳቅሁ ልብሴን ለባብሼ ወጣሁ፡፡ ይኸ ቅዠት እንጂ ህልም አይደለም እያልኩ፡፡ ቆይ ያ ሃያ ዓመት ሙሉ በቴሌቪዥን የማየው ሰውዬ በህልሜ ሳልጐበኘው በቅዠቴ መሀል ብቅ ማለቱ ደግ ሰራሁ ብሎ ነው? አክስቴ ቡና አፍልታ ቁርስ አቅርባ እየጠበቀችኝ ነበር፡፡ ተኝቼ ያየሁትን ሁሉ ነገርኳት፡፡ ካዳመጠችኝ በኋላ “አብረውህ ተሚሰሩት ፈረንጆች ተወይትኛዋ ጋር ነው የጀመርኸው?” “ምን የጀመርኩት?” “እንዲያው … ፍቅር ቢጤ” አለችኝ፤ ፈገግታዋን አክላ “እንዴት ማለት?” “አሀ! የነገርከኝ ህልም ነዋ! ዶላር፣ ፓውንድ፣ ዩሮ ማይደል ያልኸኝ? … ዙሮ ዙሮ ገንዘብ መሆኑ ማይደል?” “እና?... ቢሆንስ?” “ገንዘብ በህልም ከታዬ ልጅ ነው … ተማንኛዋም ይሁን ልጅ ልትወልድ ነው” አለችኝ “ዳሰስኩት እንጂ … በእጄ አልያዝኩትምኮ!” “ሁሉም በዳሰሳ ነው የሚጀምረው! … ሌላውን አንተ ታውቃለህ፡፡” ብላኝ እየሳቀች ወደ ጓዳ አመራች፡፡ በህልሜና በቅዠቴ መሀከል ተሰንቅሬ ሳለሁ የበረከት በላይነህ “የፈሪዎች ጥግ” የሚለው ግጥም የመጨረሻ ስንኝ ታወሰኝ፡፡ “ይህ ምስኪን ወገኔ! ላጀበው ጥያቄ እስካልተፈተሸ ቅዠት አቅፎ ያድራል - ህልሙን እየሸሸ”

Published in ልብ-ወለድ
Page 8 of 17