የዘር ቱቦ መቋጠር ህክምና ከተደረገም በኋላ እርግዝና ሊከሰት ይችላል

“ትዳር ከያዝኩ 10 ዓመት አልፎኛል፡፡ የስድስትና የአራት አመት ወንድና ሴት ልጆችም አሉኝ፡፡ ልጆቻችንን በጥሩ ሁኔታ ለማሣደግና ለማስተማር እንድንችል ቤተሰባችንን መመጠን እንደሚገባንና ተጨማሪ ልጅ መውለድ እንደሌለብን ከባለቤቴ ጋር ተመካከርንና የወሊድ መከላከያ መድሃኒት መውሰድ ጀመርኩ፡፡ በየሶስት ወሩ የሚሰጠውን መርፌ እየወሰድኩ አንድ አመት ያህል በሠላም ቆየሁ፡፡ መድሃኒቱ በሰውነቴ ላይ አንዳንድ ለውጦችን ማሳየት ሲጀምር ሃሣብ ያዘኝ፡፡ አይኔ ብዥ ይልብኝ ጀመር፣ ከፍተኛ ራስ ምታትና ትኩሳት በየጊዜው ያጋጥመኝ ጀመር፡፡ ኪሎዬ እየጨመረ ሄደ፡፡ ጉዳዩ በጣም ስላሣሰበኝ በአካባቢዬ ወደሚገኝ አንድ ክሊኒክ ሄጄ ስለ ሁኔታው አማከርኳቸው፡፡ ሰውነትሽ መድሃኒቱን በደንብ ሲለማመደው ይተውሻል አሉኝ፡፡

ህመሙ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሄዱ ቢታወቀኝም መርፌውን አቋርጬ ከባለቤቴ ጋር ተመካክረን የወሰንነውን ተጨማሪ ልጅ ያለመውለድ ውሣኔ ለማፍረስ አልፈለኩምና ቀጠልኩበት፡፡ እያደር የሚሰማኝ ስሜት እየተለወጠና እየጨመረ መምጣቱ እጅግ አሣሰበኝ፡፡ ማቅለሽለሽ፣ የምግብ ፍላጐት ማጣትና ራስ ምታት የየዕለት ህመሞቼ ሆኑ፡፡ ግራ ቢገባኝ ወደ ሆስፒታል ሄጄ ምርመራ አደረግሁ። የምርመራውም ውጤት የሁለት ወር ነፍሰጡር መሆኔን አረዳኝ፡፡ ሁኔታውን ማመን አልቻልኩም፡፡ እንዴት ይሆናል? “በመርፌ የሚሰጠውን የእርግዝና መከላከያ መድሃኒት በአግባቡና በሥነስርዓት መውሰድ ከጀመርኩ አንድ ዓመት ሆኖኛል፤ እንዴት አረግዛለሁ?” ብዬ ከሃኪሙ ጋር ሙግት ገጠምኩ። ግን ሆኗል፡፡ ምንም ማድረግ አልቻልኩም፡፡

ማርገዜን ለባለቤቴ ስነግረው ሊያምነኝ አልቻለም፡፡ ሆን ብለሽ መድሃኒት መውሰዱን (መርፌ መወጋቱን) አቁመሽ ነው እንጂ እንዴት በመድሃኒት ላይ ይረገዛል ብሎ ሞገተኝ፡፡ ስለ ጉዳዩ እንዲያስረዱት ወደ ሆስፒታል ይዤው ሄድኩ፡፡ ሐኪሞቹ እንዲህ አይነት አጋጣሚዎች ሊፈጠር እንደሚችሉ ቢነግሩትም ሊዋጥለት አልቻለም፡፡ ጊዜውን ጠብቆ ህፃኑ ተወለደ፡፡ ባለቤቴ ከእሱ ፍላጐትና ፍቃድ ውጪ በተወለደው ልጅ እምብዛም ደስተኛ አልሆነም። ምን ማድረግ እችላለሁ፡፡ የወሊድ መከላከያ እየተባለ በመርፌና በኪኒን የሚሰጡን መድሃኒት እርግዝናን አይከላከልም ማለት ነው? እንዲህ ከሆነ ደግሞ መከላከል የማይችለውን ይከላከላል እያሉ በቴሌቭዥኑና በሬዲዮ የሚጨቀጭቁን ለምንድነው?” በጥቁር አንበሣ ሆስፒታል ቅጥር ግቢ ውስጥ ልጃቸውን ለማሣከም መጥተው ያገኘኋቸውን የአንዲት እናት ቅሬታ ነው ለፅሁፌ መግቢያ ያደረግሁት፡፡

ወ/ሮ ተናኜ ታደሰ የተባሉት እኚህ እናት፤ ለእርግዝና መከላከያነት ለአንድ ዓመት ያህል የተጠቀሙበትን መርፌ በየጊዜው እየሄዱ የሚወጉት በአካባቢያቸው በሚገኝ የጤና ጣቢያ ውስጥ ነበር፡፡ ወ/ሮ ተናኜ መከላከያው በእርግጠኝነት እርግዝና እንዳይፈጠር ሊያደርግላቸው እንደሚችል በማመናቸው ሌሎች ተጨማሪ የእርግዝና መከላከያዎችን አይጠቀሙም፡፡ ሆኖም ባላሰቡትና ባልጠበቁት ጊዜ ያለ ዕቅድ ለሚከሰት እርግዝና ተጋልጠዋል፡፡ ይህ ሁኔታም ወ/ሮ ተናኜ ሙሉ በሙሉ በወሊድ መከላከያ መድሃኒቶች ላይ ያላቸውን እምነት እንዲሽሩ አድርጓቸዋል፡፡ አሁን አሁን ለወ/ሮ ተናኜ የተሻለውና ተመራጩ የወሊድ መከላከያ ዘዴ ባህላዊ ወይንም ተፈጥሮአዊ መከላከያ ዘዴዎችን መጠቀም ሆኗል፡፡ እናም ጡት ማጥባት፣ በወር አበባ ሁደት መጠቀም እና አንዳንዴ ደግሞ ከግብረሥጋ መታቀብን መርጠው እየተጠቀሙበት ይገኛሉ፡፡

የወሊድ መከላከያ መድሃኒቶች በባህላዊ፣ በተፈጥሮአዊና በሰው ሠራሽ መንገዶች እየተዘጋጁ ለተጠቃሚዎች የሚሰጡና ያልተፈለገ እርግዝና እንዳይፈጠር ለማድረግ የሚረዱ ናቸው። በባህላዊ መንገድ የሚዘጋጁ የእርግዝና መከላከያዎች አሠራራቸውና አጠቃቀማቸው ከቦታ ቦታ ይለያያል፡፡ በአገራችን በባህላዊ መንገድ የሚዘጋጁ የእርግዝና መከላከያዎች በተለይም በደቡባዊው የአገራችን ክፍል በስፋት የተለመደ ነው፡፡ በሐመርና በሱርማ ብሔረሰብች ባህል አንዲት ሴት ለአቅመ ሄዋን ስትደርስ፣ የግብረ ስጋ ግንኙነት ማድረግ ይፈቀድላታል፡፡ ከጋብቻ በፊት ማርገዝ ግን በብሔረሰቦቹ ዘንድ እጅግ የተወገዘ ጉዳይ ነው። ኮረዳዋ ከጋብቻ በፊት እንዳታረግዝ ከዕፅዋት የተዘጋጀ የወሊድ መቆጣጠሪያ መድሃኒት ይሰጣታል፡፡ ይህ ባህላዊ የወሊድ መከላከያም ኮረዳዋ ትዳር ይዛ ልጅ ለመውለድ ዝግጁ እስከምትሆን ድረስ እርግዝና እንዳይፈጠር በአስተማማኝ ሁኔታ ይከላከልላታል፡፡ የኮረዳነት ዘመኗን ጨርሳ ትዳር ስትይዝ በባህላዊ መድሃኒት ቀማሚዎች የተዘጋጀው የመድሃኒት ማርከሻ ይሰጣታል፡፡ ይህም መድሃኒቱን ስለሚያረክስላት ማርገዝ ትችላለች፡፡

ይህ አይነቱ ባህላዊ የወሊድ መከላከያ መድሃኒት በአንዳንድ ቦታዎች ላይ የተለመደ ነው፡፡ ተፈጥሮአዊ የወሊድ መከላከያ የሚባሉት ደግሞ ምንም አይነት ኬሚካል ያላቸው መድሃኒቶችን ወደ ውስጥ ሣያስገቡ በተለያዩ ተፈጥሮአዊ መንገዶች እርግዝናን መከላከል የሚያስችሉ ናቸው፡፡ ከእነዚህ መንገዶች መካከልም በወር አበባ ሁደት መጠቀም፣ የሰውነት ሙቀትንና ፈሳሽን በመቆጣጠር ግብረ ስጋ ግንኙነት መፈፀም፣ ግንኙነት ካደረጉ በኋላ የወንዱን ዘር ወደ ውጪ እንዲፈስ ማድረግና ጡት ማጥባት ተጠቃሾች ናቸው፡፡ የወር አበባ ሁደትን ለመጠቀም የሴቷ የወር አበባ መምጫ ያልተዛባና ጊዜውን በአግባቡ ጠብቆ የሚመጣ መሆን አለበት፡፡ የሰውነት ሙቀትንና ፈሳሽን በመለካት ለመጠቀም ሴቲቱ ንቁና የሰውነቷን ለውጦች በየጊዜው የምትረዳና የምትከታተል መሆን ይኖርባታል፡፡ በግንኙነት ወቅት የዘር ፍሬን ከሴቷ ማህፀን ውጪ በማፍሰስ እርግዝና እንዳይፈጠር ለማድረግ የሚያስችለው ዘዴ ሁልጊዜም አስተማማኝ ነው ማለት አይቻልም። ለዚህ ምክንያት ደግሞ የወንዱ ዘር ወንዱ ለወሲብ ከተነቃቃበት ጊዜ ጀምሮ በብልቱ ጫፍ ላይ በሚገኝ እርጥበት ውስጥ ስለሚኖርና ይህም ወንዱ የእርካታ ጫፍ ላይ ደርሶ ዘሩን ሙሉ በሙሉ ከመርጨቱ በፊት ወደ ሴቷ ማህፀን ዘሩ እንዲገባ ስለሚያደርግ እንደሆነ ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡

የማህፀንና የፅንስ ስፔሻሊስት ሐኪሙ ዶ/ር ፍፁም ተወልደ ብርሃን እንደሚናገሩት፤ በዚህ ዘዴ ከሚጠቀሙ ሴቶች መካከል ከግማሽ በላይ የሚሆኑት እርግዝና ይከሰትባቸዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በዚህ ዘዴ ለመጠቀም ወንዱ በግንኙነት ወቅት ንቁና ስሜቱን በአግባቡ ለመቆጣጠር የሚችል መሆን ይኖርበታል፡፡ በህመም፣ በሃይማኖት ጉዳዮችና በተለያዩ ምክንያቶች ሰው ሰራሹን የወሊድ መከላከያ መጠቀም ለማይችሉ ሰዎች ተፈጥሮአዊው የወሊድ መከላከያ ዘዴ ተመራጭ እንደሆነም ባለሙያው ይናገራሉ፡፡ ሠው ሠራሹ የወሊድ መከላከያ ዘዴ ደግሞ በሁለት አይነት መንገዶች የሚዘጋጅ ነው። ይህም ቋሚ የእርግዝና መከላከያና ጊዜያዊ የእርግዝና መከላከያዎች ተብሎ ይገለፃል፡፡ በአሁኑ ወቅት በስፋት ገበያ ላይ የሚገኙት የወሊድ መቆጣጠሪያዎች ሆርሞኖች እንደሆኑ የሚናገሩት ዶ/ር ፍፁም፤ የሆርሞኖቹ አሠራር በሴቶች ውስጥ ካለው ሆርሞን ጋር ተመሳሳይነት እንዳለውና ይህም የሆርሞኖቹን መጠን በማመጣጠን እርግዝና እንዳይከሰት ለማድረግ እንደሚያስችል ይገልፃሉ፡፡

ቋሚ የእርግዝና መከላከያዎች ተብለው ከሚገለፁት መካከል የዘር መተላለፍያ ቱቦዎችን መዝጋት፤ መርፌ፣ በክንድ የሚቀበሩ መድሃኒቶች፣ በማህፀን ውስጥ የሚገባው ሉፕ ሲጠቀሱ በየቀኑ የሚዋጡ ክኒኖች፣ ኮንዶም፣ ፎምና ጄሎች ደግሞ ጊዜያዊ የእርግዝና መከላከያ መድሃኒቶች ናቸው፡፡ እነዚህ መድሃኒቶች እርግዝና እንዳይፈጠር ለመከላከል ያስችላሉ ቢባልም ውጤታቸው መቶ በመቶ አስተማማኝ ነው ለማለት ግን እንደማያስደፍር ዶክተሩ ይናገራሉ፡፡ ከላይ የተጠቀሱት መድሃኒቶችን በአግባቡና በትክክለኛው ጊዜ እየወሰዱ እርግዝና ሊያጋጥማቸው የሚችሉ ሴቶች መኖራቸውን የጠቆሙት ዶ/ር ፍፁም ይህ ግን በቁጥር እጅግ አነስተኛ መሆኑን ጠቅሰዋል። መከላከያውን በአግባቡ ከወሰዱ ሴቶች መካከል 0.1 በመቶ የሚሆኑት እርግዝና ሊያጋጥማቸው መቻሉ እንግዳ ነገር አይደለም ሲሉም ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ የሚዋጥ ክኒን የሚወስዱ ሴቶች በአብዛኛው ለዚህ ችግር እንደሚጋለጡ ጠቅሰው፤ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ አብዛኛውን ጊዜ የሚዋጥ ክኒኖችን በየዕለቱ የሚወሰዱ ሴቶች መድሃኒቱን ሳያወስዱ መርሳት፣ ከወሰዱ ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ማስመለስ አይነት አጋጣሚዎች የመድሃኒቱን የመከላከል ብቃት በመቀነስ ለእርግዝና እንደሚያጋልጥ ጠቅሰዋል።

የወሊድ መከላከያ መድሃኒቶች እርግዝናን ለመከላከል ከሚሰጡት ጠቀሜታ ጐን ለጐን የሚያስከትሏቸው የጐንዮሽ ጉዳቶች መኖራቸውን የሚገልፁት ዶ/ር ፍፁም፤ ከነዚህ ችግሮች መካከልም የወር አበባ መዛባት፣ ክብደት መጨመር፣ የደም መርጋትንና ስትሮክ የደም ግፊትን፣ የካንሰር ህመሞችን ማባባስ (በተለይም የጉበትና የጡት ካንሰሮችን) ጡት አካባቢ ማወፈር፣ የወር አበባ እንዳይታይ ማድረግ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ መድሃኒቶቹ የማህፀንና የማህፀን ካንሰርን መከላከል፣ ከማህፀን ውጪ እርግዝናን መከላከል፣ የአጥንት ጥንካሬን እንዳይቀንስ ማድረግ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ የወሊድ መከላከያ መድሃኒቶች መውሰድ አደገኛ ከሚሆንባቸዉ ሴቶች መካከል የቲቢ በሽታ ያለባቸው፣ የሚያጠቡ እናቶች፣ የቆዳ ችግር ያለባቸው ሴቶች ይጠቀሳሉ፡፡

የእርግዝና መከላከያ መድሃኒቶች መቶ በመቶ እርግዝና ያስቀራሉ ማለት አይደለም በሚለው ሃሣብ በአዲስ ህይወት ሆስፒታል የማህፀንና ፅንስ ስፔሻሊስት የሆኑት ዶ/ር ካሣሁንም ይስማማሉ፡፡ እርግዝናን 100% መከላከል ያስችላል የሚባል መድሃኒት አለመኖሩን የሚናገሩት ዶክተሩ፤ በኦፕራሲዮን የዘር መተላለፊያ ቱቦዎችን እንዲቋረጡ የሚደረገው የመከላከያ ህክምና ከተሠራላቸው በኋላ እንኳን ማርገዝ የቻሉ ሰዎች መኖራቸውን ጠቁመዋል። እርግዝናን ሙሉ በሙሉ አስተማማኝ በሆነ መንገድ ለማስቀረት የሚያስችለው ዘዴ ከግብረ ሥጋ ግንኙነት መታቀብ እና ማህፀንን ማስወጣት መሆኑንም ዶክተር ካሣሁን አክለው ገልፀዋል፡፡ የወሊድ መከላከያ መድሃኒቶች መቶ በመቶ እርግዝናን መከላከል እንደሚችሉ በተለያዩ ሚዲያዎች እየተናገሩ ህብረተሰቡን ከማሣሣት የመከላከል አቅማቸው ምን ያህል እንደሆነ በግልፅ ማሣወቁ ተገቢነት ያለው ተግባር መሆኑን ባለሙያዎቹ ይጠቁማሉ፡፡

Published in ዋናው ጤና

       የውጪ ድርጅቶች በልማቱ ላይ እንቅፋት እየሆኑ ነው

          ከፈጣን ባቡር ፕሮጀክት ጋር በተያያዘ ለመንገዱ የሚያስፈልገውን መሬት ለማግኘት ከሚተገበረው የወሰነ ማስከበር ስራ ጋር በተገናኘ አድሎ እንደሚፈፀምና ተለዋዋጭ ውሳኔዎች እንደሚተላለፉ ነዋሪዎች ሲናገሩ፤ ፕሮጀክቱን በበላይነት የሚመራው የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን በበኩሉ የወሰን ማስከበሩ ስራ ለኔም የራስ ምታት ሆኗል፤ ስራዬንም እያጓተተ ነው አለ፡፡ ከሲኤምሲ አካባቢ እስከ ጦር ሃይሎች ለሚደርሰው የ8 ኪሎ ሜትር የባቡር መንገድ ፕሮጀክት በሚያስፈልገው የማስተር ፕላን ቦታ ውስጥ የተገኙ የመኖሪያ፣ የንግድ ቤቶችና ትላልቅ ህንፃዎች እየፈረሱ ሲሆን በአካባቢው ያሉ ንግድ ቤቶች በማፍረስ ሂደቱ በተለይ ከልኬት ጋር በተገናኘ በተደጋጋሚ ተለዋዋጭ የሆኑ ውሣኔዎች እየተላለፉ መሆኑ ቋሚ ወሰናችንን እንዳናውቅ አድርጎናል፤ ይህም የንግድ ስራችንን እያወከብን ነው ብለዋል፡፡ በመጀመሪያ ቀን ልኬት መሠረት አፍርሱ ከተባልን በኋላ በተወሰነልን ድንበር ላይ ራሳችንን አቋቁመን ስራችንን ስንጀምር በድጋሚ የተወሰኑ ሜትሮች አፍርሳችሁ ወደ ውስጥ አስጠጉ እንባላለን የሚሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ከዚህም ባሻገር በተመሳሳይ ክልል ውስጥ በሚገኙ ቤቶችና ህንፃዎች መካከል አድሎ ይፈፀማል፣ አንደኛው ሲፈርስ አጠገቡ ያለው ሣይፈርስ ይቀመጣል በማለት ችግሩን ይገልፃሉ፡፡ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ፍቃዱ ሃይሌ በበኩላቸው፤ በህብረተሰቡ የሚነሱት ቅሬታዎች ትክክል መሆናቸውን በመግለጽ በተለይ ተለዋዋጭ የልኬት ስራዎች ላይ የሚሰነዘረው ቅሬታ እሣቸውንም በተደጋጋሚ ከባለሙያዎች ጋር የሚያጋጫቸው ተገቢ ያልሆነ አሠራር መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ባለሙያዎቹ በማስተር ፕላኑ የተፈቀደውን 40ሜትር ስፋት ለማግኘት በሚያከናወኑት የልኬት ስራ ውስጥ ለስራው ትኩረት ሠጥቶ ሃላፊነትን ካለመወጣት ጋር የሚፈጠር ችግር እንዳለ የጠቆሙት ኢንጂነር ፍቃዱ፤ አንዴ ቁርጥ ያለ የድንበር ልኬት አለመከናወኑ በተለይ በንግድ ስራ በሚተዳደሩ ግለሰቦች ላይ ተጽእኖ እንዳለው ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ እንደሚገነዘብና ችግሩን ለመፍታት ከከተማዋ ፕላን ኢንስቲትዩት ጋር በመቀናጀት መፍትሄዎችን ለመዘየድ እየሰሩ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ለባቡር ፕሮጀክቱ ተብሎ የማስተር ፕላኑ ከሚያዘው 40 ሜትር ውጪ ተጨማሪ መሬት እንደማይወሰድ የሚናገሩት ኢንጂነሩ፤ በዚህ ክልል ውስጥ ያሉ ህንፃዎች እና ቤቶች ግን ሙሉ በሙሉ ተነሺ ናቸው ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ እንደ “ለም ሆቴል” አካባቢ ባሉ ቦታዎች ለመንገዱ በሚገነባው ማሳለጫ ምክንያት ከ40 ሜትር ሊወጣ ይችላል፡፡ ተመሳሳይ በ22 አካባቢ፣ በመገናኛ፣ በዘሪሁን ህንፃ አካባቢ፣ በሜክሲኮ እና በለገሃር ስፖርት ኮሚሽን አካባቢም መንገዱ የውስጥ ለውስጥ እና የላይ ማሳለጫዎችን አካትቶ ስለሚሰራ ከ40 ሜትር ተወጥቶ ሊሠራ እንደሚችል ኢንጂነር ፍቃዱ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ ህንፃዎችና ቤቶች ሲፈርሱ እንደ መስፈርት የሚታዩ ጉዳዮች እንዳሉ የሚገልፁት ሃላፊው፤ በዋናነት ህንፃው ቢፈርስ ያለው የኢኮኖሚ ጉዳት፣ የሚያስከትለው ውድመት እንዲሁም ማህበራዊ አገልግሎት ላይ የሚፈጥረው ጫና ከግምት ይገባል ብለዋል፡፡

ይህ ከተጠና በኋላ ትንሽ ወጪና ጉዳት ያለው ቤት ወይም ህንፃ እንዲፈርስ ሲደረግ የማፍረሱ ስልጣንም የክፍለ ከተሞች መሆኑን ገልፀዋል፡፡ በዚህ መሠረት በመንገዱ 40 ሜትር ክልል ውስጥ ያረፉ ህንፃዎችና ቤቶች ተገቢው ካሣ እየተከፈላቸው ይፈርሳሉ የሚሉት ኢ/ር ፍቃዱ፤ የመንግስት ንብረቶች የሆኑት እንደ የፍትህ ሚኒስቴር እና ልደታ ፍርድ ቤት አጥር የመሳሰሉት የአዲስ አበባ አስተዳደር ካቢኔ ባስተላለፈው ውሣኔ መሠረት፤ ያለምንም የካሣ ክፍያ እንዲፈርሱ ይደረጋል ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ ይህ የካቢኔው ውሣኔ በአንዳንድ የመንግስት ተቋማት ተቀባይነት ካላገኘ በማፍረስ ሂደቱ ላይ መጠነኛ መዘግየት እንደሚያጋጥምና ችግሩ በአጭር ጊዜ ተፈትቶ የማፍረስ ስራው እንደሚሰራ የገለፁት ኢንጂነሩ፤ በዚህ ሳቢያ ጉዳዩ እንደ አድሎአዊ አሠራር መታየት እንደሌለበት አሳስበዋል፡፡

ከኤምባሲና ከውጭ ድርጅቶች ጋር በተያያዘም ከፍተኛ ችግር እንደገጠማቸው የነገሩን የስራ ሃላፊው፤ ከሲኤምሲ እስከ ጦር ኃይሎች በሚሰራው መንገድ ላይ ውሃ ልማት አካባቢ የሚገኘው የቡልጋሪያ ኤምባሲን ጨምሮ ልደታ አካባቢ የሚገኘው ደጅ አዝማች ባልቻ ሆስፒታል በሩሲያ መንግስት ከመተዳደሩ ጋር በተያያዘ፣ ጉዳዩ ከአለማቀፍ ስምምነት ጋር የሚገናኝ በመሆኑ በስራው ላይ መዘግየት አጋጥሟል ብለዋል፡፡ ከ6 ኪሎ እስከ ጉራራ በሚሰራው መንገድ ላይ የሚገኘው የፈረንሣይ ኤምባሲም አጥሩ ከ3-5 ሜትር ወደ ውስጥ መግባት እያለበት ኤምባሲው ለማፍረስ ፈቃደኛ ባለመሆኑ ስራው እንደተጓተተ የገለፁት ኢንጂነር ፍቃዱ፤ የውጭ ድርጅቶች የሚፈጥሩት ችግር በልማቱ ላይ እንቅፋት እየሆነ መምጣቱን አስታውቀዋል፡፡ ጉዳዩን ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አሣውቀን ምላሹን ለማግኘት እየተጠባበቅን ነው ያሉት የስራ ሃላፊው፤ የቡልጋሪያ ኤምባሲ አጥር ወደ ውስጥ ፈርሶ መሠራቱ ለፕሮጀክቱ አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የደጃዝማች ባልቻ ሆስፒታል አስተዳደርም መንገዱ በኛ በኩል ማለፍ የለበትም፤ ድንበራችንንም አናፈርስም ማለታቸው ተገቢ አለመሆኑንና ይህም በፕሮጀክቱ ላይ የመዘግየት ችግር መፈጠሩን ገልፀዋል፡፡

በመስመሩ ላይ የሚፈርሱ ህንፃዎችና ቤቶች ሁሉ መታወቃቸውንና እየፈረሱ መሆኑን የተናገሩት ኢንጂነር ፍቃዱ፤ ለገሃር አካባቢ የሚገኙት የመድህን ህንፃና የባህር ትራንስፖርት ቢሮ ህንፃ መሃንዲሶች፤ ህንፃዎቹ ሳይነኩ የባቡሩ መንገድ የሚሰራበትን አማራጭ በማመላከታቸው ከመፍረስ መዳናቸውን ገልፀዋል፡፡ ቀደም ሲል በመንገዱ ላይ የተቀበሩ የውሃ የመብራትና የስልክ መስመሮችን የማዛወር ስራ እየተሠራ እንደሆነ የተናገሩት ሃላፊው፤ እስካሁን አጠቃላይ ፕሮጀክቱ ለዋናው ስራ በሚያስፈልግ ዝግጅት ደረጃ 80 በመቶው ተጠናቋል ብለዋል፡፡ “እስከዛሬ በከተማዋ ከተገነቡ ፕሮጀክቶች ከባዱና ውስብስብ የሆነው ከሲኤም ሲ እስከ ጦር ሃይሎች የሚገነባው አዲሱ የባቡርና የመደበኛ መንገድ ፕሮጀክት ነው” የሚሉት የስራ ሃላፊው፤ በ8 ኪሎ ሜትር ውስጥ ብቻ በአምስት ቦታዎች ላይ ወሎ ሠፈርና ኦሎምፒያ አካባቢ የተሰሩትን አደባባዮችና ማሳለጫ መንገዶችን የመሰሉ ይሰራሉ ብለዋል፡፡ በተጨማሪም በሁለት ቦታዎች የላይ መሸጋገሪያ ድልድይ ስራዎች ይከናወናሉ፡፡ እነዚህ ቦታዎችም መገናኛ አደባባይ፣ 22 አካባቢ፣ ኡራኤል፣ ሜክሲኮ፣ ልደታ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ ለም ሆቴልና ዘሪሁን ህንፃ አካባቢ ደግሞ የላይ መሸጋገሪያ ድልድዮች ይሰራሉ፡፡ ከዚህ ባሻገር ነባሩ የእግረኛና የመኪና መንገድ ሙሉ ለሙሉ በአዲስ መልክ እንደገና ይሰራል ብለዋል ኢንጂነር ፍቃዱ፡፡ ሌሎች መንገዶችም በቀጣይ እየተዘጉ እንደሚገነቡ ጠቁመው፤ በዘንድሮ ክረምትም ከሜክሲኮ እስከ ልደታ ያለው መንገድ ሙሉ ለሙሉ ተዘግቶ ይሰራል ብለዋል፡፡

Published in ዜና

የማይገባውን ብልጽግና ለማግኘት አስቦ ባልተሰጠው ስልጣንና ሃላፊነት የንግድና ኢንዱስትሪ ሠራተኛ ነኝ በማለት ደረቱ ላይ የተሳሳተ ባጅ አንጠልጥሎ፣ በየሱቁ እየገባ የዘይት ዋጋ በመጠየቅ “ከዋጋ በላይ ነው የምትሸጡት፤ ሱቃችሁን አሽጋለሁ” እያለ ጉቦ ሲቀበል የነበረው ወጣት በአንድ አመት ከሁለት ወር እስራት እና በ70 ብር የገንዘብ መቀጮ ተቀጣ፡፡ በመተላለፍ በፈፀመው የማታለል ወንጀል በአቃቤ ህግ ተከሶ ልደታ በሚገኘው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 12ኛ ወንጀል ችሎት ጉዳዩ የታየው የ23 ዓመቱ ወጣት ድላየሁ ቲሮሮ ኤርጊቶ አምስት ያህል ክሶች የቀረቡበት ሲሆን በአንደኛው ክስ እንደተመለከተው፤ በ10/9/05 ዓ.ም በግምት ከቀ 7 ሰአት ሲሆን በልደታ ክፍለ ከተማ ወረዳ 01/18 “ልደታ ጠበል” ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የንግድና ኢንዱስትሪ የንግድ ቁጥጥር ሠራተኛ ሳይሆን ሠራተኛ ነኝ በማለት የንግድ ቁጥጥር ባለሙያ” የሚል ባጅ አንገቱ ላይ አንጠልጥሎ ወደ አንድ ሱቅ በመግባትና የዘይት ዋጋ በመጠየቅ “ከዋጋ በላይ ነው የምትሸጠው፤ ስለዚህ ሱቁን ላሽገው ነው” በማለት 300 ብር በጉቦ መልክ ተቀብሏል የሚል ክስ ቀርቦበታል፡፡

በሁለተኛ ክስ ደግሞ በዚያኑ ቀን በግምት ከቀኑ 8 ሰዓት ሲሆን በልደታ ክ/ከተማ ወረዳ 01/18 ልዩ ቦታው አባይ ምንጭ አካባቢ፣ ያንኑ ባጅ አንጠልጥሎ ወደ ሱቅ ጐራ በማለት የዘይት ዋጋ በመጠየቅ “ከዋጋው በላይ ነው የምትሸጠው፤ ሱቅህ እንዳይታሸግ” የሚሉ አሳሳች ነገሮችን በመናገር 175 ብር ተቀብሏል፡፡ በሶስተኛ ክስ በነጋታው ከቀኑ 10 ሰዓት በተመሳሳይ ስፍራ ያንኑ ሃሰተኛ ባጅ አንጠልጥሎ አንድ ሱቅ በመግባትና የዘይት ዋጋ በመጠየቅ “ከታሪፍ በላይ እየሸጣችሁ ነው፡፡ ስለዚህ አሽገዋለሁ” በማለት 500 ብር መቀበሉን ፣ በ4ኛው ክስም በዚያኑ እለት በ10 ሰአት በዚያው ክፍለከተማ እና ወረዳ ልዩ ቦታው ቤከር ፋርማሲ አካባቢ የዘይት ዋጋ በመጠየቅና በተመሳሳይ ሁኔታ በማስፈራራት 300 ብር እንዲሰጡት መጠየቁ፣ እንዲሁም በ5ኛ ክስነት በዚያኑ ቀን ቤከር መድሃኒት ፋብሪካ አካባቢ በሚገኙ የተለያዩ ሱቆች በመንቀሳቀስ ገንዘብ የተቀበለ በመሆኑ በፈፀመው በሃሰተኛ ሰነድ መገልገል ወንጀል ተከሶ የቀረበ ሲሆን ወንጀሉ በዘጠኝ የሰው ምስክሮችና በተለያዩ የሰነድ ማስረጃዎች ተረጋግጧል፡፡ ፍርድ ቤቱም ለእያንዳንዱ ክስ የሶስት ወር እስራት መነሻ ቅጣት እርከን አድርጐ፣ ተከሳሹን ያርማል፤ ሌሎችንም ያስተምራል በማለት በአንድ አመት ከሁለት ወር እስራት እና በብር 70 መቀጮ እንዲቀጣ ውሣኔ አስተላልፏል፡፡

Published in ዜና
Saturday, 22 June 2013 10:13

“…Puberty...

በአለማችን የተለያዩ ሰነዶች እንደሚያረጋግጡት ሴቶችም ሆኑ ወንዶች ከታዳጊነት እድሜያቸው ጀምሮ የፈጸሙቸው የወሲብ ታሪኮች አሉ፡፡ ለምሳሌ እ.ኤ.አ ከ1939-2012 ዓ/ም ድረስ ከተመዘገቡት መረጃዎች ውስጥ ሁለት ታሪኮችን እናስነብባችሁ ዋለን፡፡ አንዱ በፔሩ የተፈጠረ ሲሆን ታሪኩ እንደሚከተለው ነው። .....ሕጻኑዋ የአምስት አመት ከ7 ወር እድሜ አላት፡፡ የልጅቱዋን ጤንነት በተመለከተ ወላጆችዋ ክትትል በሚያደርጉበት ወቅት እየዋለ እያደረ ሆድዋ እያደገ እየተወጠረ ይመጣል፡፡ ይህች ልጅ የተለየ ሕመም ወይንም ደግሞ እጢ በሆድዋ ውስጥ ተፈጥሮአል በሚል ወደሆስፒታል ይወስዱአታል፡፡ መልሱም ለማመን የሚያስቸግር ነበር፡፡ ለወላጆችዋ የተነገራቸው ልጅትዋ የሰባት ወር እርጉዝ እንደነበረች ነው፡፡

ወላጆች ዋም እጅግ ቢደናገጡም ቀጣዩ እርምጃ አባትየውን በአስገድዶ መድፈር ወንጀል ጥርጣሬ ወደ እስር ቤት ማስገባት ነበር፡፡ ሆኖም ግን እየተጣራ ሲሄድ ድርጊቱ የተፈጸመው ምንም በማያውቀውና የሁለት አመት ከ6 ወር እድሜ ባለው ሕጻን ወንድሙዋ መሆኑ ታውቆአል፡፡ ይህ አጋጣሚ እጅግ የሚገርም ወይንም የሚያስደነግጥ ቢሆንም እርግዝና ውን ጊዜውን ጠብቆ በሕክምና ከማዋለድ በስተቀር ምንም አማራጭ አልነበረም..... .....ሌላወ ታሪክ በራሽያ የተፈጠረ ነው፡፡ በራሽያ እርጉዝ ሆና የተገኘችው የ6 አመት እድሜ ያላት ልጅ ናት፡፡ ይህች ልጅ ያረገዘችው በአያትዋ ተደፍራ ነበር፡፡ ይህንን ድርጊት የፈጸሙት ሰው በህግ ተጠያቂ እንዲሆኑ ሲደረግ ጽንሱ ግን እንዲቋረጥ ተደር ጎአል። በአለም አቀፍ መረጃ መሰረት ሴቶቹም ሆኑ ወንዶች እድሜያቸው ከሁለት አመት ከስድስት ወር እስከ 12/አመት የሚጠጉ ከ1939 -2012 ዓ/ም ድረስ በቁጥር ወደ 250 የሚጠጉ ህጻናት ከላይ ለተጠቀሰው ድርጊት ተጋልጠዋል፡፡ ሴት እና ወንድ ህጻናቱ አስር አመት እንኩዋን ሳይሞላቸው የማርገዝና የማስረገዝ ድርጊት መፈጸማቸው ተፈጥሮ በምትሰጠው ካለእድሜ ኮረዳነትና ወይንም ጉርምስና ባህርይ ምክንያት መሆኑን ለዚህ ንባብ ማብራሪያቸውን የሰጡን ዶ/ር ድልአየሁ በቀለ ገልጸዋል፡፡

ዶ/ር ድልአየሁ በቀለ በቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ናቸው፡፡ ኢሶግ፡ Puberty... ኮረዳነት...ጎረምሳነት እንዴት ይገለጻል? ዶ/ር ድልአየሁ፡ ኮረዳነት ወይንም ጎረምሳነት ከልጅነት ወደ አዋቂነት መሸጋገሪያ የሆኑ የእድሜ መገለጫዎች ናቸው፡፡ በእድሜ ሴቶች ወደ 8 ወይንም ከ 10-11 አመት ሲደርሱ ወንዶች ደግሞ ወደ 11 አመት ሲደርሱ የሚታዩ የእድሜ ለውጦች በእንግሊዝኛው Puberty ይባላል ፡፡ በሰውነት ላይ የሚታዩ ለውጦችን በሚመለከት፡- ሴቶች ፡- የጡት መጠን መጨመር፣ በብልትና በብብት ላይ ጸጉር ማብቀል፣ የወር አበባ መታየት፣ የሰውነት ቅርጽ መቀየር፣...ወዘተ ወንዶች፡- የዘር ፍሬ ማመንጫና የብልት ማደግ፣ የብልትና ብብት ጸጉር መብቀል፣ የድምጽ መጎርነን ፣ ፐርም ማፍሰስ...ወዘተ የመሳሰሉት ነገሮች ይታያሉ፡፡ ከላይ ከተጠቀሱት በተጨማሪ የሰውነት መግዘፍ ፣ቁመት መጨመር ፣ከፊት ላይ ቡጉር ማውጣት... በፍጥነት የሚታይ ለውጥ ከመሆኑ በተጨማሪ የስነአእምሮ ወይንም የስነተዋልዶአዊ ለውጦች በታዳጊዎቹ ላይ ይታያል፡፡

እነዚህ ለውጦች የሚታዩት እድሜውን ተከትለው በሚመነጩ አዳዲስ ሆርሞኖች ምክንያት ነው፡፡ ኢሶግ፡ ለውጡን የሚያመጡት ሆርሞኖች አስቀድሞውኑ የተፈጠሩ ናቸው ወይንስ አዲስ? ዶ/ር ድልአየሁ፡ ይህንን ለውጥ የሚያመጡትን ሆርሞኖች አፈጣጠር በሴቶች ላይ ስንመለከት ከእንቁላል ማኩረቻው ወይንም ከኦቫሪ የሚመነጩ ሆርሞኖች ናቸው ፡፡ እነዚህን ሆርሞኖች የሚያመነጨው ክፍል ሴቷ ስትወለድ ጀምሮ አብሮ የሚፈጠር ነው፡፡ ነገር ግን ሆርሞኖች ስራቸውን መስራት የሚጀምሩት በአብዛኛውን ጊዜ እድሜያቸው ከ8-11 ባለው ጊዜ ሲደርስ ነው፡፡ ይህንንም እንዲያደርጉ የሚታዘዙት ከአእምሮ በሚመነጩ ሆርሞኖች አማካኝነት ነው፡፡ ኢሶግ፡ Puberty... ኮረዳነት...ጎረምሳነት የሚያስከትለው ባህርይ ምን ይመስላል? ዶ/ር ድልአየሁ፡ በኮረዳነት ወይንም ጉርምስና እድሜ ላይ የሚኖረው ባህርይ ትንሽ ለየት ያለ ነው፡፡ በመጀመሪያ ስለጉዳዩ እውቀቱ ከሌላቸው በሰውነታቸው የተለያዩ ክፍሎች እና በድም ጻቸው በሚኖረው ለውጥ ምክንያት ግራ የመጋባት ሁኔታ ይታይባቸዋል፡፡ከዚህ ውጪ ግን በዚህ እድሜ የሚታየው ...ነገሮችን የመሞከር ወይንም ፍተሻ የማድረግ ዝንባሌ ሊኖራቸው ይችላል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ተለዋዋጭ ደስተኛና ብስጩ የመሆን ባህርይ ሊኖራቸው ይችላል፡፡ ብዙ ጊዜ በባህሪያቸው መለዋወጥ እና በሚኖራቸው ተገቢ ያልሆነ ፍላጎት ምክንያትም ከቤተሰቦቻቸው ጋር መስማማት ሲያቅታቸው ይታያል፡፡

በእንደዚህ ያለው አጋጣሚ ቤተሰብ ትልቅ ድርሻ አለው፡፡ በግልጽነት ከልጆቹ ጋር መወያየት እና ስለሁኔታው በግልጽ ማስረዳት ይጠበቅበታል፡፡ ልጆቹ ይህንን ተፈጥሮአዊ ሁኔታ በሚገባ አውቀው ዝግጁ ሆነው እንዲጠባቁ የሚያስችላቸውን እውቀት ሊያገኙ ይገባል፡፡ ከቤተ ሰብ ውጪም ትምህርት ቤቶች በበኩላቸው ተገቢውን ነገር ለህጻናቱ ማስረዳት አለባ ቸው፡፡ ኮረዳነት ወይንም ጉርምስና ወሲብ ለመፈጸም ፍላጎታቸው የሚነሳሳበት ወቅት እንደመሆኑ ቤተሰብ ወይንም የሚመለከታቸው አካላት ትኩረት ሰጥተው ህጻናቱን ከተለያዩ ተላላፊ በሽታዎች ኤችአይቪን ጨምሮ ለመከላከል በሚያስችል መልኩ ምክሩን መለገስ ይገባዋል፡፡ ልጆቹ ከዚህ ድርጊት እንዲዘገዩ ወይንም ደግሞ እራስን መጠበቅ የሚቻልባቸው መንገዶች መኖራቸውን በግልጽ ከወላጆቻቸው ወይንም ከሚያምኑዋቸው ሰዎች ማግኘት አለባቸው፡፡ ይህ ካልተፈጸመ ልጆቹ ጉዳት ላይ ሊወድቁ የሚችሉበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል፡፡

ኢሶግ፡ የኮረዳነት ወይንም ጉርምስና እድሜ የሚጀምረው ከ8/አመት በሁዋላ ሲሆን ከዚያ በፊት ባለው እድሜ ወሲብ የመፈጸም ፍላጎት ሊኖር ይችላልን? ዶ/ር ድልአየሁ፡ ይህ እድሜ ከልጅነት ወደ አዋቂነት የሚሸጋገሩበት እንደመሆኑ አንዱ የሚኖረው ለውጥ የስነተዋልዶ አካላት ሁኔታ ነው። አልፎ አልፎ ግን ከዚህ እድሜያቸው አስቀድሞም ወሲብ የመፈጸም ፍላጎትም ሆነ የማርገዝ አጋጣሚ ሊከሰት ይችላል፡፡ እንዲያውም አንዳንድ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከተጠቀሱት እድሜ በታች ሆነው የወሲብ ሙከራ እና የእርግዝናው አጋጣሚም መፈጠሩን ያሳያሉ፡፡ ይህ ገጠመኝ ቅድመ ኮረዳነት ወይንም ጉርምስና የሚከሰት ይባላል ፡፡ ኢሶግ፡ በአሁኑ ዘመን የወር አበባ መምጫ እድሜ ስንት አመት ነው ? ዶ/ር ድልአየሁ፡ በአሁኑ ጊዜ በተለይም በአገራችን የወር አበባ መምጫው እድሜ እንዲህ ነወ ተብሎ በግልጽ መናገር ባይቻልም ባደጉ አገሮች ግን ከ10-11 አመት ባለው እድሜ ሴቶች ልጆች የወር አበባ ያያሉ፡፡ የወር አበባ የመምጫው እድሜ በተለያዩ የአለማችን ክፍሎች ደረጃው ይለያያል፡፡

የወር አበባ ከቤተሰብ በሚወረስ ዝርያ ምክንያት የመምጫው ጊዜ ሊረዝም ወይንም ሊያንስ ይችላል፡፡ የወር አበባ መምጫን የህብረተሰቡ የእድገት ደረጃ እና የአኑዋኑዋር ባህርይም ሊወስነው ይችላል፡፡ ባደጉት አገሮች ባለፉት ሃያ እና ሰላሳ አመታት በተደረገው ጥናት እንደታየው ከእድገት ጋር በተገናኘ የወር አበባ የመምጫው ጊዜ በየአስር አመቱ በአማካይ ሶስት ...ሶስት ወር እየቀነሰ አሁን ካለበት ደርሶአል። ስለዚህ ዋናው የቤተሰብ ውርስ ሲሆን ከዚህ ውጪ ግን የአኑዋኑዋር ሁኔታ ...ምቾት የመሳሰሉት ነገሮች ይወስኑታል፡፡ ምቾት ማጣት ወይንም ድህነት የወር አበባ መምጫውን ሊያዘገዩት ይችላሉ የሚል ግምት አለ፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

“...ሁልጊዜ ጥሩ አስተያየት የሚሰጡኝን ሁለት ሰዎች በጣም እወዳቸዋለሁ፡፡ በሚያዩኝ ጊዜ ሁሉ ...ኦ...ዛሬ በጣም ጥሩ ነሽ፡፡ እርግዝናውም ቀለል ብሎሻል፡፡ ይሄ የሆድሽ ከፍታ እኮ ከትንሽ ጊዜ በሁዋላ ይቀላል፡፡ በተለይም ሊወለድ ሲል በጣም ይቀል ሻል፡፡ አይዞሽ የሚል አስተያየትን ከእነርሱ መስማት በጣም ያስደስተኛል ...ትላለች ፡፡በአሁኑ ወቅት እርግዝናዬ 34ኛ ሳምንቱን ይዞአል የምትለው ወይዘሮ፡ በተጨማሪም እንዲህ ትላለች፡፡ “… እኔ ለነገሩ በእርግዝናው ምክንያት በሚፈጠረው ሆርሞን ምክንያት ምንም ነገር ቢነገረኝ እንዳያናድደኝ ስለምጠነቀቅ ነው እንጂ እንኩዋንስ የማይሆን ነገር ተናግረ ውኝ ቀርቶ ደህናም ነገር ቢያወሩኝ በጥርጣሬ የምቀበል ሆኛለሁ፡፡ እስቲ በዚህ ጉዳይ የተለያዩ አባባሎችን ...ማለትም ከሰዎች የወሰድኩዋቸውን አንብቡ ብላለች አሊሰን ፋክለር...፡፡ ዶ/ር መብራቱ ጀምበር ባለፈው እትም ስለ ማህጸን ውጭ እርግዝና ያብራሩትን ካስነ በብናችሁ በሁዋላ አሊሰን ፋክለር በእርግዝና ጊዜ መነገር የሌለባቸው ያለቻቸውንና ከአገር ውስጥም ልምዳቸውን ያካፈሉንን አካተን ለንባብ እንላለን፡፡

“.....እንደሚታወቀው እርግዝና የሚፈጠረው በወንዱ ዘርና በሴቷ ዘር ግንኙነት መንስኤነት ነው፡፡ይህ በጤናማ መልኩ የተፈጠረ ከሆነ የሚገኘው በዘር ማስተላለፊያ ቱቦው ላይ ነው፡፡ በዚያም የተወሰነ ቀን ካሳለፈ በሁዋላ የተወሰነ የሰውነት ገንቢ ሕዋሳቶች ደረጃ ላይ ሲደርስ ወደ ዋናው የማህጸን ክፍል ውስጥ ይገባል፡፡ በማህጸን ውስጥም እርግዝናው እስኪጨርስ እና አድ ጎም ለመወለድ እስኪደርስ ድረስ ይቆያል፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ጊዜ ይህ ሂደት ሊዛባ ይችላል፡፡ በዚህም ሳቢያ ጽንሱ ወደ ማህጸን ከመሄዱ ይልቅ የተለያየ ቦታ በመቅረት ባለበት ቦታ እድገቱን ይጀምራል፡፡ በተለይም በዘር ማስተላለፊያ ቱቦው ጫፍ ወይንም መሃል አለበለዚያም ወደ ማህጸን ተጠግቶ ሊያድግ ይችላል፡፡ ከዚህም ውጭ ጽንሱ እንደተፈጠረ ዝም ብሎ ሆድ እቃ ውስጥ በመውደቅ ሞራ ላይ ወይንም አንጀት ላይ እና በመሳሰሉት አካላት በመጠጋት በዚያው እድገቱን ሊጀምርም ይችላል፡፡.. ከላይ ያስነበብናችሁ የማህጸን ውጭ እርግዝና እንዴት እንደሚፈጠር የሚያስረዳውን ባለፈው እትም ዶ/ር መብራቱ ጀምበር ያብራሩትን ነበር፡፡ በተለይም በሆድ እቃ ውስጥ ሰለሚኖረው ከማህጸን ውጭ እርግዝና ሲገልጹ፡- “...ከማህጸን ውጭ እርግዝና ከሁለት እስከ ሶስት ወር ድረስ አደጋ የሚከሰትበት ወቅት ነው፡፡

ነገር ግን በሆድ እቃ ውስጥ የሚያርፈው ከማህጸን ውጭ እርግዝና አልፎ አልፎ እስከመጨረሻው የእርግዝና ወቅት ድረስ ደርሰው በሰላም ልጆቻቸውን የተገላገሉ አሉ፡፡በእርግጥ እርግዝናው በማህጸን ውስጥ እንደሚኖረው እርግዝና ሳይሆን አስቸጋሪና ከበድ ያለ ነው፡፡ በሆድ እቃ ውስጥ ያሉ ሌሎች አካላት ጨጉዋራ፣ ጉበት...ወዘተእንዳሉ ሆነው እርግዝናው ግን ባገኘው ክፍት ቦታ ላይ የሚቀመጥ ይሆናል፡፡ ዋናው ነገር የእንግዴ ልጁ የደም ስር ሊያገኝ እና ሊያድግ የሚችልበት ቦታ መሆን አለበት፡፡ እንግዴ ልጁ የሚመቸው ቦታ ላይ ካረፈ በሁዋላ ለልጁ ከእናቱ ደም ስቦ አጣርቶ በመመገብ እንዲያድግ ያደርገዋል፡፡ እርግዝናው በማህጸን ውስጥ ባለመሆኑ መጥፎ አጋጣሚ ነው ተብሎ ቢፈረጅም ልጁን በሰላም እስከመጨረሻው ጠብቆ መገላገል ግን እድለኝነት ይባላል፡፡ በእርግጥ ይህ ሁኔታ በቅርብ ጊዜ የተፈጸመ ሳይሆን በአሁኑ ጊዜ ያሉ ክኖሎ ጂዎች ባልነበሩበት ወቅት የነበረ አጋጣሚ ነው፡፡

በአሁኑ ጊዜ ግን አስቀድሞውኑ ጽንሱ የተፈጠረበት ስፍራ በምርመራ ስለሚታወቅ አደጋ ከማስከተሉ በፊት እርምጃ ይወሰ ዳል፡፡ አስቀድሞ በነበረው የህክምና ዘዴ ግን በሆድ እቃ ውስጥ የሚፈጠረው እርግዝና እስኪወለድ ድረስ ሊከሰት የሚችለውን አደጋ እንዳይደርስ ከመናፈቅ ባለፈ የሚደረግ ነገር አልነበረም፡፡ ጽንስ በማህጸን ውስጥም ሆነ በሆድ እቃ ውስጥ ሲረገዝ የራሱ የሆነ መሸፈኛ ይኖረዋል፡፡ ጽንስ በማህጸን ውስጥ ሲያድግ ላስቲክ መሰል በሆነ ስስ ሽፋን ውስጥ ሆኖ በሽፋኑ ውስጥ የሽርት ውሀ ከቦት ነው የሚያድገው፡፡ በእርግጥ ሽፋኑ እንደላስቲክ ስስ ሳይሆን ጠንከር ያለ እና ሞራ መሰል መልክ ያለው ነው፡፡ ይህ አፈጣጠር ጽንሱ በሆድ እቃ ውስጥም በሚፈጠ ርበት ወቅት በተመሳሳይ ሁኔታ ተሸፍኖ ስለሆነ ባለበት ቦታ ምንም ባእድ ነገር ሳያገኘው ሊያድግ ይችላል፡፡ ነገር ግን እርግዝናው ምን ያህል እንደሚቀጥል ማወቅ ስለማይቻል ዝም ብሎ እስከመጨረሻው መጠበቅ ያስቸግራል፡፡

ከማህጸን ውጭ በሆድ እቃ ውስጥ የተረገዘ ጽንስ የሚወለደው ካለምንም ችግር በኦፕራሲዮን ይሆናል፡፡ በማህጸን ውስጥ የተረገዘን ልጅ በኦፕራሲዮን ለማዋለድ በመጀ መሪያ የሆድ እቃ ከዚያ በሁዋላ ደግሞ ማህጸን ተከፍቶ ሲሆን እርግዝናው በሆድ እቃ ውስጥ ከሆነ ግን እንዲያውም በቀላሉ ሆድ እቃን ብቻ በመክፈት ማገላገል ይቻላል፡፡ የማዋለዱን ተግባር ልዩ የሚያደርገው ግን እንግዴ ልጁ በዚያው መቅረት ስለሚገባው ነው፡፡ የእንግዴ ልጅን ለማውጣት ትግል ከተፈጠረ ደም የመፍሰስ ነገር ስለሚከሰት አደጋ ላይ መውደቅን ያስከትላል፡፡ ስለዚህም እትብቱን ቆርጦ ልጁን ከማውጣትና አንባቢውን ከማጽዳት ያለፈ ምንም አይደረግም፡፡ እንግዴ ልጁ በዚያው እንዲጠፋ ይተዋል ፡፡ በማህጸን የተረገዘ ልጅ ሲወለድ የእንግዴ ልጁ በጥንቃቄ የሚወገድ እና ይቅር ቢባልም አደጋን የሚያስከትል ሲሆን በሆድ እቃ ውስጥ ግን ምንም ችግር ሳያስከትል በራሱ ጊዜ እንዲጠፋ ይደረጋል፡፡

ከማህጸን ውጭ የተረገዘ ልጅ እንቅስቃሴው ፊት ለፊት በቀላሉ የሚታይ ነው፡፡ ምክንያቱም በማህጸን ውስጥ እንዳለው ልጅ በሁለተኛ ደረጃ በማህጸን ግድግዳ ተሸፍኖ ስለማይገኝ ነው፡፡ በምጥ መውለድን በሚመለከትም በሆድ እቃ የሚኖር እርግዝና በትእግስት በሚጠበቅበት ዘመን በክሊኒክ በሚቆጠረው የጊዜ ቀመር በመመስረት በኦፕራሲዮን እንዲወለድ ይደረጋል እንጂ እንደ መደበኛው እርግዝና ምጥን መጠበቅ አይቻልም፡፡ ከማህጸን ውጭ እርግዝና በዘር ማስተላለፊያ ቱቦ ውስጥም ይሁን በሆድ እቃ ውስጥ ሲፈጠር አደጋ የሚያስከትልበት ሁኔታ መኖሩ እርግጥ ነው፡፡ በተለይም ከሁለት እስከሶስት ወር ድረስ ባለው ጊዜ ከሚከሰተው አደጋ ዋናው የደም መፍሰስ ነው፡፡ የዚህም ምክንያቱ ጽንሱ ያለበት ቦታ እስከመጨረሻው ስለማያሳድገውና መቀደድ ስለሚጀምር ነው፡፡

ይህንን ሁኔታ የሚያባብሰውም እርግዝና በሚፈጠርበት ጊዜ እርግዝናው ባለበት አካባቢ እርግዝናውን ለማሳደግ የደም ስሮች በብዛት ስለሚፈጠሩ ጽንሱ ያለበት ቦታ ሲፈነዳ ደም በኃይል እንዲፈስ ስለሚያደርግ ነው ፡፡ይህ የደም መፍሰስም ሴትየዋን እስከሞት ሊያደርስ የሚችል ነው፡፡ ከማህጸን ውጭ እርግዝናን አስቀድሞ መወቅ የሚቻልባቸው ምልክቶች አሉ፡፡ እርግዝናው መኖሩ ከተረጋገጠ በሁዋላ ከማህጸን ደም መፍሰስ ሊጀምር ይችላል፡፡ ከእምብርት በታች ባለው የሰ ውነት ክፍል ሕመም ሊኖር ይችላል፡፡ እግርን የመያዝ አይነት ስሜት ሊኖር ይችላል፡፡ እርግዝናው ውጥረቱ እየጨመረ ሲሄድ ከመፈንዳቱ በፊት የተገለጹት ስሜቶች ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡በእርግጥ ሌሎች የጤና ሁኔታዎችም ተመሳሳይ የህመም ምልክቶችን ሊያሳዩ እንደሚችሉ መገመት ያስፈልጋል፡፡

ማንኛዋም ሴት የወር አበባዋ በሚቀርበት ጊዜ ገና ከጅምሩ ወደሐኪም ዘንድ ቀርባ ምርመራዋን ብትጀምር ሁኔታው አደጋ ከማስከተሉ በፊት እርምጃ ለመውሰድ ያስችላል እንደ ዶ/ር መብራቱ ጀምበር የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ማብራሪያ፡፡ ለእርጉዝ ሴቶች ሊነገሩ የማይገባቸው ነገሮች፡- እርግጠኛ ነሽ ...መንታ ላለማርገዝሽ? አንቺ ...ሆድሽ ሊፈነዳ ደርሶአል እኮ...ከዚህ በላይ መቆየት የምትችይ ይመስልሻል? የእኔ ሚስት አኮ አምስት ልጅ ወልዳለች፡፡ ግን እንዳንቺ ሰውነቷ አልተበላሸም፡፡ ለመሆኑ ሐኪምሽ ምን ይልሻል? በእርግጥ ሙሉ በሙሉ ጤነኛ ነሽ? አትናደጂ፡፡ ግን እርግዝና ነው ወይንስ ሌላ ነገር? መልክሽ እንዲህ የጠቆረው በጤና ነው? መልክሽ እንዲህ እስኪጠፋ ድረስ ያሳበጠሽ በእርግጥ እርግዝናው ብቻ ነው? አንቺ...ምን መሰልሽ? ምነው እርግዝናው ቢቀርስ? ...ወዘተ ከላይ የተጠቀሱትንና መሰል ነገሮችን ለእርጉዝ ሴቶች ማቅረብ ተገቢ አይደለም፡፡ በተለይም አርግዞ በመውለድ ዙሪያ ሊያጋጥሙ የሚችሉ አደጋዎችን ከመንገር ይልቅ ሴትየዋ በትክክል ወደሐኪም ሄዳ እርዳታ ማግኘት የምትችልበትን መንገድ መምከር ይገባል፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

አፍሪካ የመጀመሪያውን የነፃነት ዳንሷን ትደንስ በነበረበት በ1960ዎቹ የመጀመሪያ አመታት ሴዳር ሴንጐር፣ ሁፌት ቧኘ፣ ክዋሜ ንክሩማህ፣ ጋማል አብደል ናስር፣ አህመድ ሴኩቱሬ፣ ሞዲቦ ኬታ፣ ጆሞ ኬንያታ፣ ጁልየስ ኔሬሬ፣ ካሙዙ ባንዳና የመሳሠሉ መሪዎች ነበሯት፡፡ መስራች አባቶችና የአፍሪካ የመጀመሪያው ትውልድ መሪዎች የሚል የተለየ መጠሪያ ያተረፉት እነዚህ መሪዎች ታላቅ ክብርና ዝና የተጐናፀፉ ነበሩ፡፡ ዘጠና አምስት በመቶ የሚሆኑትን የአፍሪካ ሀገራት ለበርካታ ዘመናት ሰጥለጥ አድርገውና አንበርክከው በቅኝነት ከገዙት ሁለት የምዕራብ አውሮፓ ሀገሮች አንዷ ፈረንሳይ ናት፡፡ “ከዝንጀሮ ቆንጆ ምን ይመራርጧል” ካልተባለ በስተቀር የፈረንሳይ የቅኝ አገዛዝ ዘይቤ “አመሳስለህ ግዛ (Assimilation) በመባል የሚታወቅና ዋነኛ የቅኝ አገዛዝ ተፎካካሪዋ ከነበረችው ከእንግሊዝ “የከፋፍለህ ግዛ” የቅኝ አገዛዝ ዘይቤ የተለየ ነበር፡፡

ፈረንሳይ በቅኝ አገዛዟ ስር የነበሩትን በሚሊዮን የሚቆጠሩ የምዕራብ አፍሪካ ዜጐችን “አመሳስለህ ግዛ” በሚለው የአገዛዝ ዘይቤዋ አማካኝነት “እናንተ ጥቁር ሆናችሁ እንጂ ፈረንሳውያን ናችሁ እኮ! … ባለ ጥቁር ቆዳ ፈረንሳያውያን!” እያለች ታጃጅላቸው ነበር፡፡ በ1958 ዓ.ም የፈረንሳይ የአራተኛው ሪፐብሊክ መንግስት ፈርሶ ስልጣን እንደለቀቀ፣ በፕሬዚዳንት ሻርል ደጐል የሚመራው የአምስተኛው ሪፐብሊክ መንግስት ስልጣኑን ያዘ፡፡ አዲሱ የፕሬዚዳንት ደጐል መንግስትም በመላ አፍሪካ ቀስ በቀስ እየተቀጣጠለ የመጣውን የነፃነት ትግል የመጨረሻ መዳረሻውን በሚገባ በመገምገም፣ በምዕራብ አፍሪካ ያለውን የቅኝ ግዛት የበላይነትና ብሔራዊ ጥቅሙን ጠብቆ ለማቆየት ያስችለኛል ያለውን አዲስ አይነት ስልት ቀየሰ፡፡ በዚህም መሠረት የፍራንኮ-አፍሪካ ኮሙኒቲ እንዲመሠረት የሚጠይቅ አንቀጽ የተካተተበትን አዲስ ህገ መንግስት ስልጣን በያዘበት አመት አርቅቆ አቀረበ፡፡

ይህንን ተከትሎም ፕሬዚዳንት ደጐል፣ የፈረንሳይ ቅኝ የሆኑ የምዕራብ አፍሪካ ሀገራት መስከረም 28 ቀን 1958 ዓ.ም በህገመንግስቱ ላይ ህዝበ-ውሳኔ በማካሄድ፣ የፍራንኮ-አፍሪካ ኮሙኒቲ መመስረትን ይደግፉ አይደግፉ እንዲያሳውቁ ቀጭን ትዕዛዝ አስተላለፉ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ፣ የፕሬዚዳንት ደጐል ትዕዛዝ የፈረንሳይ ቅኝ ለነበሩት በርካታ የምዕራብ አፍሪካ ሀገራት ህዝቦች ቀላል አልነበረም፡፡ ህዝበ-ውሳኔውም ተራ ህዝበ-ውሳኔ አይደለም፡፡ ፈረንሳይ ልትመሠርተው ያቀደችው የፍራንኮ-አፍሪካ ኮሙኒቲ አባል ለሆኑ የአፍሪካ ሀገራት የሚፈቅደው የውስጥ አስተዳደር ነፃነትን ብቻ እንጂ የሚኖሩት በፈረንሳይ ሉአላዊነትና የበላይነት ስር በመሆን ነው፡፡ የዚህ ኮሙኒቲ አባል ለመሆን በጄ የማይልና የማይቀበል ሀገር ግን ነፃነቱን መጐናፀፍ ቢችልም ከፈረንሳይ መንግስት ሽራፊ ሳንቲም ማግኘት አይችልም፡፡

ፕሬዚዳንት ደጐል፤ በቅኝ አገዛዝ ሀገራቸው ለምታስተዳድራቸው የምዕራብ አፍሪካ ሀገራት ያቀረቡት ምርጫ ከእነዚህ ሁለቱ አንዱን መምረጥ ነበር፡፡ ለፈረንሳይ መንግስት ባላቸው ታላቅ ከበሬታና ታማኝነት እንዲሁም የፈረንሳይን እርዳታ ላለማጣት ከነበራቸው ከፍተኛ ፍላጐት የተነሳ፣ በፈረንሳይ ቅኝ አገዛዝ ስር ከነበሩትና ህዝበ ውሳኔውን መስከረም 28 ቀን 1958 ዓ.ም ካካሄዱ የምዕራብ አፍሪካ ሀገራት ውስጥ አብዛኞቹ ህዝበ ውሳኔውን በመደገፍ፣ የአዲሱ የፍራንኮ-አፍሪካ ኮሙኒቲ አባል ለመሆን ድምፃቸውን ሰጡ፡፡ “የፈረንሳይ እርዳታ ባፍንጫዬ ይውጣ! ነፃነት ወይም ሞት!” በሚል የፈረንሳይን ህገመንግስት በህዝበ ውሳኔ በመቃወም ነፃነቷን ለመጐናፀፍና ሉአላዊነቷን ለማረጋገጥ በቁርጠኝነት ብቻዋን የቆመችው ምዕራብ አፍሪካዊት ሀገር ጊኒ ነበረች፡፡ ከዚህ አቋምና ውሳኔ ጀርባ የነበሩት ግንባር ቀደም ታጋይ መሪ ደግሞ ጐልማሳው አህመድ ሴኩቱሬ ነበሩ፡፡

የጊኒ የነፃነት ትግልና የመጀመሪያው የጊኒ የድህረ ነፃነት መሪ የነበሩት አህመድ ሴኩቴሬ፤ በወቅቱ ከነበሩት የምዕራብ አፍሪካ የመጀመሪያው ትውልድ መሪዎች ጋር ሲወዳደሩ በአብዛኛው የተለዩ ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ በተለይ ፈረንሳይ “ባለጥቁር ቆዳ ፈረንሳዊ የበኩር ልጆች” እያለች በፍቅር ታንቆለጳጵሰውና በመንግስቷ ውስጥ የምኒስትርነት ማዕረግ አጐናጽፋቸው ከነበሩት ከሴኔጋሉ ፕሬዚዳንት ሴዳር ሴንጐርና ከኮትዲቯሩ ፕሬዚዳንት ፌሊክስ ሁፌት ቧኘ ጋር የሚመሳሰሉ አልነበሩም፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ እንደ ሴንጐርና ሁፌት ቧኘ ከሀብታም ቤተሠብ የተወለዱና የታወቁ ቱጃር አልነበሩም፡፡ ይልቁንስ ብን ካለ መናጢ ደሀ ቤተሠብ የተገኙና የልጅነት እንዲሁም የአፍላ ጉርምስና ጊዜአቸውን በከፋ ድህነት ውሰጥ ያሳለፉ መሪ ነበሩ፡፡ ሴኩቱሬ እንደ ሴንጐርና ሁፌት ቧኘ በፈረንሳይና በሴኔጋል በሚገኙ ምርጥ የፈረንሳይ ትምህርት ቤቶች ውስጥ እየተማሩ ያደጉ ሰውም አልነበሩም፡፡ በአመለካከታቸውም ቢሆን “ባለ ጥቁሩ ቆዳ ፈረንሳዊ” የሚለውን የፈረንሳይ ቅኝ አገዛዝ እምነትና አስተሳሠብ አጥብቀው የሚቃወሙ የለየላቸው የጊኒ ብሔርተኛና ፓን አፍሪካኒስት መሪ ነበሩ፡፡

በፖለቲካውም ረገድ ጠንካራ ፀረ ፈረንሳይ ቅኝ አገዛዝ አቋም የነበራቸውና ከፈረንሳይ ቅኝ አገዛዝ በመላቀቅ፣ ነፃነታቸውን ለመጐናፀፍና ለኡላዊነታቸውን ለማስከበር የጣሩ መሪ ናቸው፡፡ ፕሬዚዳንት አህመድ ሴኩቱሬ፤ ወደ ስልጣን የመጡበት መንገድም ቢሆን ሴንጐርና ሁፌት ቧኘ በመጡበትና በአንፃራዊነት የተሻለና ደልዳላ በነበረው የአፍሪካ ልሂቃን ዝግ የፖለቲካ አለም አማካኝነት ሳይሆን ረጅም፣ ወጣ ገባና፣ አስቸጋሪ በነበረው የሰራተኛ ማህበራት ፖለቲካ በኩል ነበር፡፡ የጊኒን የሠራተኛ ማህበራት መሠረት በማድረግ የጊኒን ዲሞክራቲክ ፓርቲ (ጊዲፓ) ጠንካራ የህዝብ ንቅናቄ ፓርቲ እንዲሆን በሚገባ አስችለውታል፡፡ ይሄው ፓርቲያቸው በ1957 ዓ.ም በተካሄደው ህዝባዊ ምርጫ፤ ከስልሳ መቀመጫዎች ሀምሳ አምስቱን እንዲያሸንፉ በማድረጋቸው፣ ገና በሰላሳ አምስት አመት የጐልማሳነት እድሜአቸው የጊኒ ጠቅላይ ሚኒስትር መሆን ችለዋል፡፡ የለየላቸው የክዋሜ ንክሩማህ አድናቂ የነበሩት ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ፤ ከፈረንሳይ የፍራንኮ አፍሪካ ኮሙኒቲ ይልቅ ለፓን አፍሪካን አንድነት መመስረት ድምፃቸውን ከፍ አድርገው የሚያሰሙ መሪ ነበሩ፡፡

በዚህ አቋማቸው የተነሳም የፕሬዚዳንት ደጐልን እቅድ “አዲስ የንግድ ምልክት የተለጠፈበት የድሮ ያረጀ ሸቀጥ ነው” በማለት በሰላ ሂስ ይተቹና ይነቅፉ ነበር፡፡ ፕሬዚዳንት ደጐል ያቀረቡትን ህገ መንግስት፣ የፈረንሳይ ቅኝ የሆኑ የምዕራብ አፍሪካ መንግስታት በህዝበ ውሳኔ እንዲደግፍ ሲያደርጉት የነበረውን ቅስቀሳ አጠናቀው ነሀሴ 25 ቀን 1958 ዓ.ም የጊኒ ዋና ከተማ ኮናክሪ ሲገቡ፣ ጠቅላይ ምኒስትር ሴኩቱሬ የተቀበሏቸው ከአየር ማረፊያው እስከ ቤተ መንግስቱ ድረስ ባለው ረጅም አውራ ጐዳና ግራና ቀኝ “ነፃነት! ነፃነት! ነፃነት ወይም ሞት!” እያሉ በከፍተኛ ድምጽ መፈክር የሚያሰሙ ጊኒያውያንን በማሰለፍ ነበር፡፡ ለፕሬዚዳንት ደጐል ክብር ተብሎ እድሜ ጠገብ በሆነው ነጩ የስብሰባ አዳራሽ ውስጥ በተካሄደው ልዩ ስነስርአት ላይ ባደረጉት ንግግር፣ የፈረንሳይን የቅኝ አገዛዝ ታሪክ እየዘረዘሩ፣ ጊኒ የፍራንኮ አፍሪካ ኮሙኒቲን ከመቀላቀሏ አስቀድሞ ከቅኝ አገዛዝ ሙሉ በመሉ ነፃ መሆን እንደምትሻ አቋማቸውን በማያሻማ ቋንቋ በግልጽ አሳወቁ፡፡ ቀጠሉናም ከፊትለፊታቸው የቀመጡትን የፈረንሳይ ፕሬዚዳንት ደጐልን በጣታቸው እያመለከቱ፣ በወቅቱ የፀረ ቅኝ አገዛዝ ትግል ውስጥ በዋናነት ጐልቶ የሚጠቀሰውንና እሳቸውንም የግንባር ቀደም ፀረ ቅኝ አገዛዝና የነፃነት ታጋይ ክብር ያጐናፀፋቸውን ንግግር ተናገሩ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር አህመድ ሴኩቱሬ፣ በከፍተኛ ስሜት ተውጠው “እኛ ጊኒአውያን በባርነት ከሚገኝ ምቾትና ድሎት ይልቅ ነፃነታችንን ተጐናጽፈን ብንራብ ይሻለናል” በማለት ተናገሩ፡፡

ከፕሬዚዳንት ደጐልና አብረዋቸው ከነበሩት ረዳቶቻቸው በስተቀር በአዳራሹ የነበሩት ጊኒአውያን ከመቀመጫቸው በመነሳት በከፍተኛ የድጋፍ ስሜት ለደቂቃዎች ያልተቋረጠ ጭብጨባ አጨበጨቡላቸው፣ ጭብጨባው ጋብ እንዳለም ሴኩቱሬ ድምፃቸውን ከፍ አድርገውና የግራ እጃቸውን ጨብጠው ወደ ላይ በማንሳት “ነፃነት! ነፃነት! ነፃነታችንን አሁኑኑ! ነፃነት ወይም ሞት!” በማለት መፈክራቸውን በመደጋገም አሰሙ፡፡ የስብሰባው አዳራሽ በከፍተኛ የድጋፍ ጩኸትና ጭብጨባ በድጋሚ ለደቂቃዎች ተናወጠ፡፡ የሴኩቱሬን ንግግር በሬዲዮ ያዳመጡና በስሚ ስሚ የደረሳቸው ጊኒአውያን ከያሉበት በመሰባሰብ በአውራ ጐዳናዎች ላይ “ነፃነት! አሁኑኑ ነፃነት ወይም ሞት! ከባርነት ምቾት ይልቅ የነፃነት ረሀብ ይሻለናል!” እያሉ መፈክር በማሰማት፣ በተለይ ዋና ከተማዋን ኮናክሪን ቀውጢ አድርገዋት አመሹ፡፡ መስከረም 28 ቀን 1958 ዓ.ም በተካሄደው ህዝበ ውሳኔም ጊኒያውያን በጠቅላይ ምኒስትር አህመድ ሴኩቱሬ እየተመሩ ለፍራንኮ - አፍሪካ ኮሙኒቲ መመስረት ከፍተኛ የተቃውሞ ድምፃቸውን ሰጡ፡፡

ይህን ካደረጉ አራት ቀናት በሁዋላም ጥቅምት ሁለት ቀን 1958 ዓ.ም አህመድ ሴኩቱሬ፣ ጊኒ ከፈረንሳይ ቅኝ አገዛዝ መላቀቋንና ነፃና ሉአላዊ ሀገር መሆኗን ለመላው ህዝባቸው አወጁ፡፡ ይህ የነፃነት አዋጅ ከታወጀበት ቀን ጀምሮ ለተከታታይ አስራ አንድ ቀናት በመላ ጊኒ የሆነው ነገር ሁሉ ታሪክ ነው፡፡ መላ ጊኒያውያን ከሊቅ እስከ ደቂቅ በያሉበት በነቂስ በመውጣት “ነፃነት ለዘለአለም ይኑር! ከዘለአለም ባርነት የአንድ ቀን ነፃነት! ሴኩቱሬ ማለት ነፃነት ማለት ነው! ሴኩቱሬ የነፃነታችን አባት ነው! ሴኩቱሬ ለዘለአለም ይኑር!” የሚሉ መፈክሮችን በማሰማት አውራጐዳናዎችንና አደባባዮችን አጣበዋቸው ከረሙ፡፡ እነዚህ መፈክሮች በቀይ ቀለም የተፃፈባቸውን ባነሮች በዋና ዋና አደባባዮችና አውራ ጐዳናዎች ላይ ሰቀሉ፡፡ በመቶ ሺ የሚቆጠር የሴኩቱሬ ምስል ያለባቸው ካናቴራ፣ ሸሚዝና ቀሚሶች ህፃን አዋቂ ሳይለይ በድፍን ጊኒ መሠራጩት ቻለ፡፡ እነዚህን ልብሶች የለበሱ ጊኒያውያንም ለቀናት ሴኩቱሬንና ነፃነትን የሚያሞግሱ የትግልና የድል መዝሙሮችን በመዘመር ሲደንሱ ባጁ፡፡ በጠቅላይ ምኒስትር ሴኩቱሬ ንግግር እጅግ እንደተዋረዱና የፕሬዚዳንትነት ክብራቸው ክፉኛ እንደተነካ የቆጠሩትና ከአብዛኞቹ የፈረንሳይ ቅኝ ከነበሩ የምዕራብ አፍራካ ሀገራት ተለይታ ጊኒ ነፃነቷን በመምረጧ ልባቸው ሀይለኛ ቂም የቋጠረው የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ሻርል ደጐል፣ የበቀል ቅጣታቸውን በሴኩቱሬና በጊኒ ላይ ማሳረፍ የጀመሩት አገሪቷ ነፃነቷን እንዳወጀች አንዲት ቀን እንኳ ሳይውሉና ሳያድሩ ነበር፡፡

ፕሬዚዳንት ደጐል በመጀመሪያው ቀን በወሰዱት እርምጃ፣ ፈረንሳይ ለጊኒ የምትሰጠው ሰብአዊና የልማት እርዳታ ሙሉ በሙሉ መቋረጡን የሚገልጽ ባለ ሶስት መስመር ደብዳቤ በመፃፍ ሴኩቱሬ ለሚመሩት አዲሱ የጊኒ መንግስት አስታወቁ፡፡ በሁለተኛው ቀንም ፈረንሳውያን የመንግስት ሰራተኞች፣ ህዝብና ሀገር በመጠበቅ ላይ የነበሩ ፈረንሳውያን ፖሊሶችና ወታደሮች፣ እንዲሁም ለጊኒያውያን የህክምና የአገልግሎት ሲሰጡ የነበሩ ወታደራዊና ሲቪል ዶክተሮች፣ ነርሶችና ሌሎች የህክምና ባለሙያዎች ጊኒን ለቀው ባስቸኳይ እንዲወጡ አዘዙ፡፡ በሶስተኛው ቀን ደግሞ ፈረንሳውያን ኢንጅነሮች፣ ቴክኒሻኖች፣ መምህራን፣ የአስተዳደር ባለሙያዎችና ነጋዴዎች ባስቸኳይ ጊኒን ለቀው እንዲወጡ ትእዛዝ ሰጡ፡፡ ትዕዛዙን ተከትለውም ሶስት ሺ የሚሆኑ ፈረንሳውያን ባለሙያዎች በአንድ ቀን መሸከም የሚችሉትን ንብረት ተሸክመው፣ ያልቻሉትን ደግሞ ሰባብረው ጊኒን ለቀው ወጡ፡፡ እነዚህም ሆኑ እነዚህን ተከትለው በተከታታይ ጊኒን ለቀው የወጡት ፈረንሳውያን ባለሙያዎች አወጣጣቸው ሰላማዊና ጤነኛ አወጣጥ አልነበረም፡፡ በመንግስት ስራ ላይ ተሰማርተው የነበሩት፣ የመንግስትን ፋይሎችና መዛግብቶችን ሰብስበው አቃጠሉ፡፡

የቢሮ ወንበርና ጠረጴዛዎችን ሰባበሩ፡፡ ስልኮችን ነቃቀሉ፡፡ የኤሌክትሪክ ሀይል ማመንጫና ማስተላለፊያ ገመዶችን መነቃቀልና መበጣጠስ ብቻ ሳይሆን አምፑሎችን ሳይቀር አወላልቀው ወሰዱ፡፡ ሲቪልና የጦር ሀይሉ ዶክተሮችም አንዲት ቅንጣት ክኒን ሳትቀር የነበረውን መድሀኒትና የህክምና መገልገያ መሳሪያዎችን በሙሉ ሙልጭ አድርገው ጭነው ወጡ፡፡ የፖሊስ አባሎችም ከሚሰሩባቸው የፖሊስ ጣቢያ ቢሮዎች ነቅለው መውሰድ ያልቻሉትን በሮችና መስኮቶችን እንዳልነበሩ አድርገው ሰባበሯቸው፡፡ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥም በተለያየ መንግስታዊና የግል የስራ መስክ ተሠማርተው የነበሩ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ፈረንሳውያን ጊኒን ለቀው ጥርግ አሉ፡፡ ከወር በኋላ ኮቴአቸው ያስነሳው አቧራ ገለል ሲል የፕሬዚዳንታቸውን ትዕዛዝ በመጣስ ጊኒን ለቀው ላለመውጣት በመወሰን በበጐ ፈቃደኝነት ለማገልገል በኮንናሪ ከተማ የተገኙ ማተባቸውን ያልበጠሱ ፈረንሳውያን አንድ መቶ ሀምሳ ብቻ ነበሩ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ፣ የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ሻርል ደጐል የሰነዘሩት የበቀል ዱላ በጊኒ ህዝብ ላይ ያሳረፈው ቁስል ህመሙ አንጀት የሚያንሰፈስፍ ነበር፡፡ ጊኒ ፈረንሳዮቹ ጥለዋት ሲወጡ እነሱን ተክቶ የሚያገለግል የተማረና በወጉ የሰለጠነ የሰው ሀይል ጨርሶ አልነበራትም፡፡

ፕሬዚዳንት ደጐል ይህን እርምጃ የወሰዱትም የጊኒን ጠቅላላ ሁኔታ በደንብ ስለሚያውቁት ነበር፡፡ እናም ፈረንሳዮቹ ከያሉበት ተጠራርተው ጊኒን ጥለው ውልቅ ሲሉ የጤና፣ የትምህርትና ሌሎች መንግስታዊ አገልግሎቶች በአንዴ ተቋረጡ፡፡ የህዝብ ፀጥታና ደህንነት ጥበቃ ቆመ፡፡ የጊኒ ድንበርም ያለ አንዳች ጥበቃ ወናውን ቀረ፡፡ ጊኒ ከቅኝ ግዛት ተላቃ ነፃነቷን መጐናፀፏና ሉአላዊ ሀገር መሆን መቻሏ የፈጠረባትን ደስታ በወጉ እንኳ አጣጥማ ሳትጨርስ ብርክ ያዛት፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ እንደነገሩ የተጠጋገነ አንድ የቆዳ ወንበርና ያረጀ ጠረጴዛ ብቻ ባለው ኦና ቢሮአቸው ውስጥ ከወዲያ ወዲህ እየተንጐራደዱ የሚይዙትንና የሚጨብጡትን አጡ፡፡ ምንም እንኳ ፕሬዚዳንት ደጐልን ከቅስቀሳ ዘመቻቸው ሲመለሱ ና ብለው ጠርተው፣ አዳራሽ ሙሉ ሰው በተሰበሠበበት የሰላ ትችትና ወቀሳ በማውረድ እንዳስቀየሟቸው ቢያውቁም፣ በጊኒና በእርሳቸው ላይ ጨክነው ይህን የመሰለ እጅግ አስከፊ ቅጣት ይጥላሉ ብለው ጨርሰው አልገመቱም ነበር፡፡ ቀሪውን ሳምንት እንመለስበታለን፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

በብራዚል አስተናጋጅነት ለሚካሄደው 20ኛው ዓለም ዋንጫ በአፍሪካ ዞን ለሚደረገው የመጨረሻ ዙር የደርሶ መልስ ማጣርያ ለማለፍ ነገ በአዲስ አበባ ስታድዬም የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ደቡብ አፍሪካን በወሳኝ ግጥሚያ ሊገናኝ ነው፡፡ በ10 ምድቦች በሚደረገው የአፍሪካ የምድብ ማጣርያ በ5ኛ ዙር ግጥሚያዎች ሲቀጥል የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ነገ ደቡብ አፍሪካን የሚያሸንፍ ከሆነ 10 ቡድኖች ለሚሳተፉበት እና የአፍሪካን ተወካይ 5 ብሄራዊ ቡድኖች ለሚለየው የመጨረሻ ዙር የደርሶ መልስ ማጣርያ ማለፉን ያረጋግጣል፡፡ ደቡብ አፍሪካ በዚሁ ጨዋታ የኢትዮጵያን መሪነት በመንጠቅ ከምድብ 1 የሚያልፈው ቡድን በምድብ ማጣርያው የመጨረሻ 6ኛ ዙር ግጥሚያዎች እንዲወሰን ተስፋ ታደርጋለች፡፡

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በነገው ጨዋታ ድል ካደረገ ምድብ 1 በመሪነት ማጠናቀቁን ከ6ኛው ዙር የምድብ ማጣርያ ግጥሚያዎች በፊት የሚያረጋግጥ ሲሆን ከሜዳው ውጭ ከሴንተራል አፍሪካ ሪፖብሊክ ጋር የሚያደርገው ጨዋታ መርሃ ግብሩን ለመጨረስ ብቻ የሚያደርገው ይሆናል፡፡ ከሳምንት በፊት በምድብ 1 የ4ኛ ዙር የምድብ ማጣርያ ግጥሚያዎች ላይ ኢትዮጵያ ከሜዳዋ ውጭ ቦትስዋናን 2ለ1 በማሸፍ መሪነቷን ስታጠናክር፤ ሁለቱን ጎሎች ያስቆጠሩት ሳላሃዲን ሰኢድ እና ጌታነህ ከበደ ደግሞ በምድብ ማጣርያው የኮከብ ግብ አግቢዎች ደረጃ መሪነቱን ይዘዋል፡፡ ደቡብ አፍሪካ በካሜሮኗ ከተማ ያውንዴ ሴንተራል አፍሪካ ሪፖብሊክን 3ለ0 በማሸነፍ በነገው ጨዋታ ኢትዮጵያን የምትፎካከርበትን ተስፋ አለምልማለለች፡፡

ከኛ ዙር የምድብ ማጣርያ ግጥሚያዎች በፊት ኢትዮጵያ በምድቧ ባደረጋቻቸው 4 ጨዋታዎች 3 ድልና 1 አቻ ውጤት በማስመዝገብ በ10 ነጥብና በ4 የግብ ክፍያ ስትመራ ደቡብ አፍሪካ በ8 ነጥብና በ5 የግብ ክፍያ በ2ኛ ደረጃ ትከተላለች፡፡ የደቡብ አፍሪካ ብሄራዊ ቡድን እስከ ሳምንቱ አጋማሽ ድረስ በካሜሮን ያውንዴ ቆይታ ነበረው፡፡ ከትናንት በስቲያ በዱዋላ የመጨረሻ ልምምዳቸውን ያደረጉት ባፋና ባፋናዎች ትናንት አዲስ አበባ ገብተዋል፡፡ ለነገው ጨዋታ ደግሞ ዛሬ በአዲስ አበባ ስታድዬም የመጨረሻ ልምምድ ይሠራሉ፡፡ የደቡብ አፍሪካ ብሄራዊ ቡድን ትናንት አዲስ አበባ ከመግባቱ በፊት ኢትዮጵያ ቦትስዋናን 2ለ1 ያሸነፈችበትን ጨዋታ ቪድዮ በትኩረት ሲያጠኑ ነበር፡፡ የደቡብ አፍሪካ ብሄራዊ ቡድን በነገው ጨዋታ ኢትዮጵያን ባልተጠበቀ ብቃት በማሸነፍ የምድቡን መሪነት ሊነጥቅ እንደሚችል አንዳንድ የአገሪቱ መገናኛ ብዙሃናት ሁኔታውን በመሪ ርእስ በመግለፅ ቢዘግቡም ሌሎች ዘገባዎች ደግሞ ኢትዮጵያ በሜዳዋ በከፍተኛ ብልጫ አሸንፋ ምድቡን በመሪነት ማጠናቀቋን እንደምታረጋግጥ በዓለም ዋንጫ ለመሳተፍ ጊዜው የኢትዮጵያ ሊሆን እንደሚችል በመገመት ትንተናቸውን አሰራጭተዋል፡፡

በነገው ጨዋታ ዙርያ ለአንባቢዎቹ የውጤት ግምት እንዲሰጡ እድል ሰጥቶ የውጤት ትንበያዎችን በድረገፁ ይፋ ያደረገው ጎል የአሸናፊነቱ እድል በሜዳዋ ለምትጫወተው ኢትዮጵያ ሙሉ ለሙሉ ማጋደሉን አመልክቷል፡፡ በጎል ድረገፅ በቀረቡ 3 ዋና የውጤት ትንበያዎች መሰረት ኢትዮጵያ ደቡብ አፍሪካን 2 ለ0 እንደምታሸንፍ የገመቱ 33.9 በመቶ፤ 3ለ1 እንደምታሸንፍ የገመቱ 16.95 በመቶ እንዲሁም 2ለ1 እንደምታሸንፍ የገመቱ 15.25 በመቶ የድምፅ ድርሻ ወስደዋል፡፡ ከዓመት በፊት በምድብ ማጣርያው የመጀመርያ ግጥሚያ ደቡብ አፍሪካ በሜዳዋ ሮያል ባፎኬንግ ስታድዬም ኢትዮጵያን ባስተናገደችበት ወቅት ግጥሚያው 1ለ1 አቻ ተለያይተውበታል ይህ ውጤት ደቡብ አፍሪካ ለአራተኛ ጊዜ ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ የነበራትን ዓላማ አጣብቂኝ ውስጥ የከተተ ከመሆኑም በላይ የደቡብ አፍሪካ እግር ኳስ ፌደሬሽን ሃላፊዎችን ለውዝግብ ከመዳረጉም በላይ በወቅቱ የባፋና ባፋና አሰልጣኝ ለነበሩት ፒትሶ ሞሲማኔ መባረር መንስኤ እንደነበር ይታወሣል፡፡ በነገው ጨዋታ የደቡብ አፍሪካ ብሄራዊ ቡድን በኢትዮጵያ ከተሸነፈ ምናልባትም ለ56 ዓመቱ አሰልጣኝ ጎርደን ሌጀሰንድ መባረር ምክንያት እንደሚሆን እየተገለፀም ነው፡፡

የባፋና ባፋና ተጨዋቾች ለወሳኙ ጨዋታ ስላደረጉት ዝግጅት እና ስለሚጠብቃቸው ፈተና ሰሞኑን ሲናገሩ የሰነበቱ ሲሆን ከእነሱም መካከከል አጥቂው ቶኬሎ ራንቲ እና አማካዩ ሲፍዌ ሻባላላ ይጠቀሳሉ፡፡ የአጥቂ መስመር ተሰላፊው ቶኬሎ፤ ራንቲ በሰጠው አስተያየት‹ በወሳኙ ጨዋታ ላይ ማግኘት ያለብንን ውጤት ማንም ሊያስታውሰን ወይም በግፊት ሊያስረዳን አይገባም፡፡ ማሸነፍ የሚኖረውን ጠቀሜታ ሁላችንም ስለምናውቅ መነሳሳታችን አይቀርም› ሲል ተናግሯል፡፡ የነገውን ጨዋታ የሞት ሽረት ፍልሚያ ነው ያለው አጥቂው ቶኬሎ ግጥሚያው የምንሰጥምበት ወይም የምንዋኝበት ነውም ብሏል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ከ2 ዓመት በፊት ባስተናገደችው 19ኛው የዓለም ዋንጫ የውድደሩን የመክፈቻ ግብ ያስቆጠረው አማካዩ ሲፍዌ ሻባላላ በበኩሉ‹ የኢትዮጵያ ቡድን ካለው ወቅታዊ አቋምና በሜዳው ከመጫወቱ አንፃር የማይበገር ሊሆን ይችላል፡፡

በደጋፊያቸው ፊት በመጫወታቸው ከጨዋታው መጀመርያ ፊሽካ አንስቶ በከፍተኛ ወረራ ሊያጠቁን ይችላሉ፡፡ በዚህ ሳንሸበር ተረጋግተን ጨዋታውን ለመቆጣጠር በመትጋት የምንፈልገውን ውጤት ለማግኘት በህብረት እንሰራለን› ሲል አስተያየቱን ተናግሯል፡፡ የዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ፌደሬሽኖች ማህበር ፊፋ የአፍሪካ ዞን የምድብ ማጣርያ ከዓመት በፊት ሲጀመር ስለምድብ 1 ብሄራዊ ቡድኖች ባቀረበው ትንተና ምድቡን በመሪነት ለማጠናቀቅ እድል ያላት ደቡብ አፍሪካ እንደሆነች ገልፆ ነበር ያልተጠበቀ ውጤት የምታስመዘግበው ቦትስዋና እንደሆነች ያመለከተው ድረገፁ የምድቡን አላፊ የሚወስነው ወሳኝ ጨዋታ ደቡብ አፍሪካ ከቦትስዋና የሚያደርጉት ፍልሚያ እንደሆነም አብራርቶ ነበር፡፡

ከ1 ዓመት በኋላ የምድብ ማጣርያው ጉዞ በኋላ ግን የፊፋ ኦፊሴላዊ ድረገፅ እንደገመተው ሳይሆን ቀርቷል፡፡ ይህን ግምት ፉርሽ ያደረገው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ውጤታማነት ሲሆን ከምድቡ በመሪነት ለማለፍ ሰፊ እድል ከመያዙ ባሻገር የምድቡን አላፊ የሚወስነው ጨዋታ ነገ ኢትዮጵያ ከደቡብ አፍሪካ የሚገናኙበት ጨዋታ ሆኗል፡፡ በአፍሪካ ዞን በሚቀጥሉት የ5ኛ ዙር የምድብ ማጣርያዎች በምድብ 1 እንደምትገኘው ኢትዮጵያ ከመጨረሻው ዙር የምድብ ማጣርያ ግጥሚያ በፊት በየምድባቸው በመሪነት ለመጨረስ እድል ያላቸው ሶስት አገራት በምድብ 7 ግብፅ፤ በምድብ 2 ቱኒዚያ እና በምድብ 10 ሴኔጋል ናቸው፡፡ በተቀረ በምድብ 3 ኮትዲቯር ወይም ሞሮኮ፤ በምድብ 4 ጋና ወይም ዛምቢያ፤ በምድብ 5 ጋቦን ወይም ቦትስዋና፤ በምድብ 6 ናይጄርያ፤ በምድብ 8 አልጄርያ እንዲሁም በምድብ 9 ካሜሮን በመሪነት የምድብ ማጣርያውን ለማጠናቀቅ የሚችሉበት ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ ብራዚል ከዓመት በኋላ ለምታስተናግደው 20ኛው ዓለም ዋንጫ አፍሪካን ለመወከል እንደሚበቁ ግምት ካገኙ 5 ብሄራዊ ቡድኖች ደቡብ አፍሪካ ብዙ ግምት ያገኘች ነበረች፡፡

ከ10000 በላይ የውጤት ሁኔታዎችን በማገናዘብ እና በማስላት በአንድ ድረገፅ በቀረበ ትንበያ ደቡብ አፍሪካ ለዓለም ዋንጫው ያላት የማለፍ እድል 23.77 በመቶ ሲገመት ለኢትዮጵያ የተሰጠው ግምት ግን 5.8 በመቶ ነው፡፡ በሌላ በኩል አንድ የስፖርት ዘገባ በሰራው ግምታዊ ትንተና ወደ ዓለም ዋንጫው የሚያልፉ 5 ብሄራዊ ቡድኖችን ለመለየት በሚያስችለው የምድብ ማጣርያው በመሪነት ሊያልፉ የሚችሉትን 10 ብሄራዊ ቡድኖች ሲገምት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንንም አካትቷል፡፡ ይሄው ድረገፅ ለዓለም ዋንጫው የመጨረሻ ዙር የደርሶ መልስ ማጣርያ የሚያልፉ ቡድኖችን ዘርዝሮ ድልድሉ በሁለት ምድብ ሲከፍል በመጀመርያው በፊፋ ከፍተኛ ደረጃ ያላቸውን ኮትዲቯር፤ ናይጄርያ፤ አልጄርያ፤ ቱኒዚያ እና ዛምቢያን በሌላ ምድብ ደግሞ ካሜሮን፤ ግብፅ፤ ሴኔጋል፤ ኮንጎ እና ኢትዮጵያ ሊሆኑ እንደሚችሉ ገምቷል፡፡

  • ኳሷን ማሸነፍ ማለት ለእያንዳንዷ ኳስ ትኩረት መስጠት ነው
  • አጥቂዎች አንድ እድል ሲያገኙ አንድ ጎል ለማግባት ማሰብ አለባቸው
  • አጥቂዎች ወደ ጎል የሚሞክሯቸውን ኳሶች መሬት አስይዘው ይምቱ
  • ለዓለም ዋንጫ ማለፍ ማለት የአገር ገጽታን ሊቀይር የሚችል ነው


ኳስ ተጨዋች ነበር፡፡ ከ16 ዓመት በፊት በአርሰናል ተጠባባቂ ቡድን ውስጥ ለ6 ወራት የሙከራና የልምምድ ጊዜ አሳልፏል፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስም ተጨዋች ነበር፡፡ ዛሬ ግን ያሬድ ተስፋዬ የተዋጣለት ነጋዴ ሆኗል፡፡ በመዝናኛ ዘርፉ ላይ የሚሰራው ያሬድ፤ የታዋቂው ፕላቲኒዬም የምሽት ክለብ ባለቤት ነው፡፡ ፕላቲኒዬም የፈርኒቸር ማምረቻ የሚባል ድርጅትም አለው፡፡ ቢቲ ትሬዲንግ በተሰኘ የኤሌክትሮኒክስ እቃዎች አስመጭ ኩባንያ ውስጥም ከቤተሰቡ ጋር እንደሚሰራ ይናገራል፡፡ አሁን ያሬድ ወደ ስፖርቱ ለመመለስ አስቧል፡፡ ይህን ሃሳቡን በመደገፍም አብሮት የተማረው ጋዜጠኛ አማን ከበደ እያበረታታው እንደሆነም ይናገራል፡፡ “ካሳለፍኩት የተጫዋችነት ህይወት፣ ከነበረኝ ልምድና ተሞክሮ በመነሳት በኢትዮጵያ እግር ኳስ የለውጥ ምዕራፍ የበኩሌን አስተዋጽኦ ለማበርከት እፈልጋለሁ” ይላል፡፡ በክለብ ማኔጅመንት፣ በተጨዋች ወኪልነት፣ በስፖንሰርሺፕና ማርኬቲንግ እንቅስቃሴዎች የመስራት እቅዶች አሉት፡፡

ዛሬ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የደረሰበት የብቃት ደረጃ ለስፖርቱ ዕድገት የሚያግዙ ተግባራትን ለማከናወን መልካም አጋጣሚ መፍጠሩን የሚገልፀው ያሬድ፤ በተጫዋችነት ዘመኑ ሊያሳካው ይሻው የነበረውን ህልም በመጪው ትውልድ እውን ሆኖ ማየት ይፈልጋል፡፡ የብሔራዊ ቡድኑ ውጤታማነት የኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገት መገለጫ እንደሆነም ያምናል፡፡ እኔ ከያሬድ ተስፋዬ ጋር ሰሞኑን ጭውውት ሳደርግ ኢትዮጵያውያን የእግር ኳስ አፍቃሪዎች ሁሉ ወሬያቸው ነገ ብሄራዊ ቡድናችን ከደቡብ አፍሪካ ጋር የሚያደርገው ጨዋታ እንደሚሆን ቅንጣት ጥርጣሬ የለኝም፡፡ ያሬድ ተስፋዬም ያወጋኝ ስለዚሁ ጉዳይ ነው፡፡ ስለ ብሄራዊ ቡድኑ አባላትና ስለእግር ኳስና ስለነገው ግጥሚያ የተጨዋወትነውን እነሆ፡፡
ነገ ዋልያዎቹ ከባፋና ባፋና ጋር በሚያደርጉት ጨዋታ ምን ትጠብቃለህ?
ከደቡብ አፍሪካ ጋር የሚደረገው ጨዋታ በጣም ወሳኝ ነው፡፡ ዋልያዎቹ በዚህ ግጥሚያ ትልቅ አገራዊ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ የሚገቡት ወደ ጦርነት ሜዳ ነው ማለት ይቻላል፡፡ የአገራቸውን ገፅታ የሚለውጡበት፣ የህዝባቸውን አንድነት የሚያጠናክሩበት፣ የኢትዮጵያውያን የዕድገት ተስፋ የሚያለመልሙበት ውጤት ነው የምጠብቀው፡፡
በነገው ጨዋታ የሚገኝ ውጤት እኮ ለዓለም ዋንጫ ማለፍ ያስችላል ማለት አይደለም፡፡ የነገውን ጨዋታ በአሸናፊነት ቢወጣ እንኳን ቡድኑን ገና ሌላ ምእራፍ ይጠብቀዋል ፡፡ ከአፍሪካ 10 ሃያል ቡድኖች አንዱ ሆኖ ብራዚል ለምታስተናግደው 20ኛው ዓለም ዋንጫ ለማለፍ በመጨረሻው የደርሶ መልስ ጨዋታ ላይ ውጤት ማምጣት የዋልያዎቹ ፈተና ይሆናል፡፡ ከደቡብ አፍሪካ ጋር የሚደረገው ፍልሚያ ወሳኝነት ታዲያ ምኑ ላይ ነው?
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በነገው ጨዋታ ደቡብ አፍሪካን አሸንፎ፣ ለመጨረሻው የጥሎ ማለፍ ውድድር ከሚበቁ የአፍሪካ 10 ብሔራዊ ቡድኖች አንዱ ለመሆን መብቃቱ ያጓጓል፡፡ ወደ ዓለም ዋንጫ የሚያሳልፈው የ10 ብሄራዊ ቡድኖች የደርሶ መልስ ትንቅንቅ የነገውን ወሳኝ ፍልሚያ በድል በማጠናቀቅ የሚደረስበት ምእራፍ ነው፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ የነገውን ጨዋታ በድል ለመወጣት ቅድሚያ ትኩረት በመስጠት ስለነገው ነው ማሰብ ያለበት፡፡ ቀጣዩ ጨዋታ ከማን ጋር እንደሚሆን በማናውቀው ጉዳይ ላይ ማሰብ የለብንም፡፡ የነገውን ማሸነፍ ዓለም ዋንጫ እንደመግባት እንዲቆጥሩት ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ በኋላ ሌላ ወሳኝ ምእራፍ አለ ብሎ መግባት ጥሩ አይሆንም፡፡ የነገውን ወሳኝ ጨዋታ አሸንፎ በማለፍ ነው ለመጨረሻው ምእራፍ የሚደረሰው፡፡

በመጀመርያ ደረጃ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በሜዳው በሚያደርገው ጨዋታ እንደሚያሸንፍ ተስፋ ተፈጥሮ መሸነፍ ማለት ለተጫዋቾቹም ሆነ ለስፖርት አፍቃሪው ሞራል የሚነካ ነው፡፡ ከደቡብ አፍሪካ ጋር 1ለ1 ከሜዳው ውጭ አቻ ወጥቶ የተመለሰ ቡድን፣ እዚህ አገሩ ላይ የሚሸነፍበት ምንም አይነት ምክንያት አይኖርም፡፡
ዋልያዎቹ ለዚሁ ወሳኝ ጨዋታ ምን ማድረግ አለባቸው? በእርግጥ በደጋፊያቸው ፊት እንደመጫወታቸው ማሸነፍ እንደሚችሉ ለመገመት አይከብድም፡፡ ይሁንና የጨዋታው ወሳኝነት የሚፈጥረው ጫና ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ በዚህ ላይ ደቡብ አፍሪካ በዚሁ ጨዋታ ነጥብ ይዞ ለመውጣት በከፍተኛ ፍላጎት ዝግጅት ስታደርግ ቆይታለች፡፡ ከሳምንት በፊት ሴንትራል አፍሪካ ሪፐብሊክን 3ለ0 ማሸነፏም ስጋት መፍጠሩ አይቀርም ፡፡ አንተ እንደ ስፖርት አፍቃሪ፤ እንደ ቀድሞ ኳስ ተጨዋችነትህ እና ከነበረህ ልምድ አንፃር ምን ትላለህ?
ሁሉም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጨዋቾች እና አባላት ከፍተኛ የሞራል መነቃቃት እና ትኩረት ያስፈልጋቸዋል፡፡ በጨዋታው እያንዳንዷን ኳስ ለ90 ደቂቃዎች አሸንፈው መጫወት አለባቸው፡፡ ኳስ ከተነጠቁ መንጠቅ፣ ከነጠቁ ደግሞ ወደ ተግባር መለወጥ አለባቸው፡፡ እያንዳንዷን ኳስ ለማሸነፍ መፋለም አለባቸው፡፡ ኳሷን ማሸነፍ ማለት ለእያንዳንዷ ኳስ ትኩረት መስጠት ነው፡፡

በእያንዳንዷ ቅፅበት ያለውን ሁኔታ ሁሉም ተጨዋቾች እኩል ትኩረት በመስጠት ሙሉ 90 ደቂቃዎችን መጫወት አለባቸው፡፡ ዋልያዎቹ ጨዋታቸውን እዚህ አገራቸው እንደማድረጋቸው፤ ፊሽካ ከተነፋባት የመጀመርያዋ ደቂቃ አንስቶ ጫና ፈጥረው መጫወት አለባቸው፡፡ በሜዳቸው እየተጫወቱ መከላከል የለባቸውም፡፡ አገር ላይ መጫወት ያለው ጥቅም ለማግባት መጫወት ነው፡፡ የደቡብ አፍሪካ ቡድን ከኢትዮጵያ የምድቡን መሪነት ለመንጠቅ ከጅምሩ የሚጫወተው በማጥቃት ስለሚሆን፤ ያን በመከላከል ለማቆም መሞከር ለተደጋጋሚ ጥቃቶች ራስን ማጋለጥ ነው፡፡ ለማሸነፍ ማግባት አለብን፡፡ ለማግባት ደግሞ ማጥቃት አለብን፡፡ ዋልያዎቹ ጨዋታውን ሙሉ ለሙሉ መቆጣጠር አለባቸው፡፡ የኢትዮጵያ ቡድን በምድቡ ከሴንትራል አፍሪካ ሪፐብሊክ ጋር ከሜዳው ውጭ ስለሚያደርገው ጨዋታ በፍፁም ማሰብ የለበትም፡፡ በነገው ጨዋታ ውጤቱን አሳምሮ ምድቡን በመሪነት ለመጨረስ መታሰብ አለበት፡፡ ማንም ተጨዋች ግጥሚያው የአገር ጉዳይ መሆኑን አምኖ መቶ በመቶ ብቃቱን ማሳየት አለበት፡፡ ይህን ለመወጣት የማይችል፤ በቂ እና የተሟላ ብቃት ለእለቱ ማበርከት እንደማይችል የሚያስብ ተጨዋች ካለ፣ ከእኔ ይልቅ እከሌ ቢገባ ይሻላል ብሎ በግልፅ ሃሳቡን ለአሰልጣኙ ማንፀባረቅ አለበት፡፡ ይህ ወሳኝ ምእራፍ የሙከራ ጊዜ አይደለም፡፡ ሜዳ የሚገቡ ተጨዋቾችም ያላቸውን ሙሉ ብቃት በመጠቀም፤ የላቀ የቡድን ስራ እና ቁርጠኝነት በማሳየት አስፈላጊውን ውጤት ለማስመዝገብ በልበሙሉነት መሰለፍ አለባቸው፡፡ ለብሔራዊ ቡድኑ ዋናው የስነልቦና ጥንካሬ የሚሆነው ለግጥሚያው በቂ ትኩረት ከማድረግ ባሻገር ለተጋጣሚው ቡድን ቀላል ግን ጠንቃቃ ግምት መስጠት ነው፡፡
ምንም አይነት ስህተት መሠራት የለበትም፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ደቡብ አፍሪካን በሜዳዋ ገጥሞ 1ለ1 አቻ መውጣቱ ይታወሳል፡፡ በርግጥ በዚያ ጨዋታ የተገኘው ውጤት በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ በርካታ ኢትዮጵያውያን ስታድዬም ገብተው ለዋልያዎቹ የሰጡት ድጋፍ አስተዋጽኦ ሊኖረው ይችላል፡፡ በነገው ጨዋታ ግን ዋልያዎቹ በሜዳቸው እንደመጫወታቸው የመላው ኢትዮጵያዊ ድጋፍ ይበልጥ የጨመረ ይሆናል፡፡ ሌላው ለዋልያዎቹ የስነልቦና ጥንካሬ የሚሆነው የሚያስመዘግቡት ውጤት ትልቅ የታሪክ ምእራፍ መሆኑን ማሰብ ነው፡፡ ሁሉም የብሔራዊ ቡድኑ አባላት ለነገው ጨዋታ ከሰሞኑ ዝግጅታቸውም በላይ ዛሬ ልዩ ትኩረት እና በምክክር የተደገፈ የመጨረሻ ዝግጅት ያድርጉ፡፡ በቂ ልምምድ ሰርተውና ጥሩ እረፍት አድርገው ለነገው ፍልሚያ በተነቃቃ ስሜት፤ በጥሩ የአካል ብቃት እና ቅልጥፍና ተሳስበው በአገር ፍቅር ስሜት መስራት አለባቸው፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአስተማማኝ ሁኔታ ለማሸነፍ ይችል ዘንድ እንደ ተመልካች ምን አይነት ሃሳቦችን ትሰጣለህ?
ለማሸነፍ ከተፈለገ ሶስት መሰረታዊ ነገሮችን መተግበር አለበት ብዬ ነው የማስበው፡፡ እነዚህ ተግባራዊ ሲደረጉ የማሸነፍ እድሉ 99 በመቶ ይሆናል፡፡ በመጀመርያ ደረጃ ማንኛውም ተጨዋች ያለበትን የስነልቦና ችግር ከአሰልጣኙ ጋር ከተወያየ እና በግልፅነት ከተመካከረ ለአገር የሚሆን ውጤት ያስገኛል፡፡ ሁለተኛ 90 ደቂቃዎቹን በሙሉ ትኩረት ሰጥቶ ከኳስ ጋር እና ከኳስ ውጭ በመንቀሳቀስ ከተጫወተ ግጥሚያውን ሙሉ ለሙሉ መቆጣጠር ይችላል፡፡ ሶስተኛ የቡድኑ የአጥቂ መስመር ተሰላፊዎች የሚሰጧቸውን ያለቁ ኳሶች አማራጭ እንደሌለ በማሰብ ሌላ እድል አገኛለሁ በማለት ሳይዘናጉ፣ ከመጀመርያው ያገኟትን ኳስ ወደ ግብ መሬት አሲይዘው ከሞከሩ ውጤታማ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ አጥቂዎች ወደ ጎል የሚሞክሯቸውን ኳሶች መሬት አስይዘው ይምቱ የምለው ያለምክንያት አይደለም፡፡
ከመረብ የመዋሃድ እድል ያላቸው ኳሶች መሬት ለመሬት የሚመቱ ናቸው፡፡ ወደ ላይ የሚነሳ ኳስ የመግባት እድሉ ጠባብ ነው፡፡ አጥቂዎች አንድ እድል ሲያገኙ አንድ ጎል ለማግባት ማሰብ አለባቸው፡፡ ይህ አይነቱን ሙከራ ለሙሉ 90 ደቂቃዎች መቀጠል ደግሞ ውጤታማ ያደርጋል፡፡ በእርግጥ በወቅቱ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ካየኋቸው ለውጦች የመጀመሪያው የአጥቂዎች የአጨራረስ ብቃት ማደግ ነው፡፡ ዛሬ በብሔራዊ ቡድን ያሉ አጥቂዎች ጐል የማግባት ብቃታቸውና በቅጽበታዊ ውሳኔ ውጤት የማግኘት ክህሎታቸው ተለውጧል፡፡ በተለይ ቡድኑ ከሜዳ ውጭ በሚያደርጋቸው ጨዋታዎች አጥቂዎች ጐል የማስቆጠር ድፍረት ማዳበራቸው ጉልህ ለውጥ ነው፡፡ በአጠቃላይ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ውጤት እያማረ እና እየተለወጠ የመጣው የአጥቂዎች አጨራረስ ዕድገት በማሳየቱ ነው፡፡ ለዚህ የአጥቂዎች ውጤታማነት ፈር ቀዳጅነት ሚና የተጫወተው ሳላሃዲን ሰኢድ ነው፡፡ የእሱ የአጨራረስ ድፍረት እና በየግጥሚያዎቹ የሚያስቆጥራቸው ወሳኝ ጐሎች ብሔራዊ ቡድን አሁን ለደረሰበት ደረጃ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ ሌሎች በሱ መስመር የሚሰለፉ የቡድኑ ተጨዋቾችን በማነቃቃትም አርአያ ሆኗል፡፡
የነገው ጨዋታ በድል ተጠናቀቀ እንበል፤ ቀጣዩ ወሳኝ ምእራፍ ከዚያ በኋላ ይመጣል፡፡ አሁን ብዙዎቹ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች እንደሚገልፁት፣ የኢትዮጵያ ጊዜ ሆኖ ብሄራዊ ቡድኑ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ለዓለም ዋንጫ ቢያልፍ ስኬቱ ምን ትርጉም ይኖራዋል?
የማንም ተጨዋች፣ የየትኛውም እግር ኳስ ወዳድ ህዝብ አገር ህልምና ተስፋ የዓለም ዋንጫን መሳተፍ ነው፡፡ የብሔራዊ ቡድኑ ለዓለም ዋንጫ ማለፍ መቻል የእግር ኳሱን እድገት በአስደናቂ ሁኔታ የሚያፋጥነው ይሆናል፡፡የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫ ሲያልፍ ለስፖርቱ ዕድገት በር ከፋች የሚሆኑ በርካታ እድሎች እና ሁኔታዎች ይፈጠራሉ፡፡ ለምሳሌ ያህል ቡድኑ ለዓለም ዋንጫ ካለፈ በኋላ በአገሪቱ በሚካሄደው የሊግ ውድድር ከፍተኛ የሆነ የፉክክር ደረጃ ይፈጠራል፡፡ ይህም ክለቦች በበቂ ሁኔታ ተደራጅተው እና በተጨዋቾች ስብስብ ተጠናክረው ወደ ውድድር የሚገቡበትን ሁኔታ ያነቃቃል፡፡ በየክለቡ ያሉ ተጨዋቾች በዓለም ዋንጫ በሚሳተፈው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለመመረጥ ከፍተኛ ትጋትና ብቃት ማሳየታቸውም ሌላው ለውጥ ነው፡፡
ባለሀብቶች የአገሪቱ እግር ኳስ ለዓለም ዋንጫ በመብቃቱ በስፖርቱ ዘርፍ መዋዕለ ንዋያቸውን ለማፍሰስ፣ ክለቦችን በመግዛት እና በገንዘብ በመደገፍ ለመስራት በቀላሉ የሚነሳሱበትን ሁኔታም ይፈጥራል፡፡ ኩባንያዎች የተሰማሩባቸውን የኢንቨስትመንት መስኮች ለማስተዋወቅና ከስፖርቱ ለውጥ ጋር የንግድና የእድገት እንቅስቃሴያቸውን ለማስተሳሰር ፍላጎት ያድርባቸዋል፡፡ ስታድዬሞችም በስፖርት አፍቃሪዎች መጥለቅለቃቸው አይቀርም፡፡ ለምን ቢባል ህዝብ ወደ ስታድዬሞች የሚተመው በዓለም ዋንጫ የሚሳተፉ ተጨዋቾችን ለመመልከት ስለሚሆን ነው፡፡ የዓለም ዋንጫው ስኬት የመንግስትንም ትኩረት የሚስብ ነው፡፡ የተጀመሩ መሰረተ ልማቶች በአፋጣኝ እንዲያልቁም ያበረታታል፡፡ በመጀመርያ ደረጃ ውጤቱ መንግስትና ህዝብን በማገናኘት ለአገር ልማት እና እድገት በጋራ መተሳሰብ እና በበጎ ስሜት እንዲሰሩ ተፅእኖ ማሳደሩ አይቀርም፡፡ በአጠቃላይ ለዓለም ዋንጫ ማለፍ ማለት በውስጥም ሆነ በውጭ የአገርን ገጽታ ሊቀይር የሚችል ነው፡፡

“ዘፈኖቼ ህፃናትን የሚያሳድጉ ናቸው” - ጃ ሉድ

የሬጌ ሙዚቃ አቀንቃኙ ጃ ሉድ፤ በዳግማይ ትንሳኤ እለት በላፍቶ ሞል “ድግስ ቁጥር ሁለት” የተሰኘ ኮንሠርት ለማቅረብ ዝግጅቱ ከተጠናቀቀና ትኬት ተሸጦ ካለቀ በኋላ ድንገተኛ የመውደቅ አደጋ ደርሶበት ኮንሰርቱ መሰረዙ ይታወሳል፡፡ መውደቁ ካደረሰበት የጤና መታወክ ካገገመ በኋላ ግን በተለያዩ የውጭ አገራት ተዘዋውሮ ኮንሰርቶችን በማቅረብ የዛሬ ሳምንት ወደ አገሩ ተመልሷል፡፡
ባለፈው ቅዳሜ ምሽትም በተሰረዘው ኮንሰርት ምትክ “ድግስ ቁጥር ሁለት”ን በላፍቶ ሞል አቅርቧል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ድምፃዊውን ከኮንሰርቱ በፊት አግኝታው ስለውጭ አገር ኮንሰርቱ፣ ስለአዘፋፈን ስልቱ፣ በኮንሰርቱ መሠረዝ ስለደረሠው ኪሳራና ሌሎች ጉዳዮች አነጋግራዋለች፡፡ እንደ ዘፈኖቹ ዘና የሚያደርገውን ጭውውት እንድታነቡት ተጋብዛችኋል፡፡

 

የት የት ነበር የሙዚቃ ድግስ ስታቀርብ የቆየኸው?
ምን እባክሽ እኔ እኮ አላውቃቸውም… አንዱ ስዊዘርላንድ ነው፤ የመጨረሻውን አሪፍ እና የሚያምር የሙዚቃ ጊዜ ያሳለፍኩት ስዊዲን ነበር፡፡ ከዛ በፊት እንግሊዝ ነበርኩኝ፡፡ ለነገሩ እንግሊዝን ከበፊት ጀምሮ አውቃታለሁ፡፡ ግን ምን አለፋሽ… ስንገበገብ ሄጄ ስንገበገብ መጣሁ፡፡
እንዴት?
የዚህ አገር አየር እዚያ የለማ! እስካሁን የረገጥኩበት ቦታ የኢትዮጵያ አየር የለም፡፡
አየሩ ብቻ ነው ያልተመቸህ ወይስ ሌላም ነገር አለ?
አየሩ ነው፤ ብቻ ኢትዮጵያን ስለቃት የሆነ የሆነ ነገር እሆናለሁ፡፡ አይደላኝም፡፡ ነገር ግን ስራዬን በቆንጆ ሁኔታ ሰርቻለሁ፡፡
ኮንሠርትህን ያሳረግኸው ስውዲን ላይ ነው፡፡ የሠው አቀባበል እንዴት ነበር?
ኦ! የስውዲኑ በጣም ያምራል፤ ከምነግርሽ በላይ አሪፍ ነበር!
ስለተሠረዘው ኮንሠርትህ ብናወራስ?
ይቻላል! ምን ገዶኝ …
አወዳደቅህ እንዴት ነበር? ምን አጋጠመህ?
አወዳደቄ ትንሽ አስደንጋጭ ነበር፡፡ ድንጋጤውን የበለጠ ያደረገው የኔ መውደቅና መታመም ሳይሆን የሠዎች መጉላላት አስጨንቆኝ ስለነበር ነው፡፡ ነገር ግን ችግሬ አሳማኝ ነበር፤ አሁን እንደምታይው እየደረቀልኝ ነው (ጉልበቱ ላይ ያለውን በመድረቅ ላይ ያለ ቁስል ሱሪውን ሰብስቦ እያሳየኝ) አወዳደቄ ከቤቴ ጋር ተጋጭቼ ነው፡፡ ቤቱ አዲስ ስለነበር ደረጃ የረገጥኩ መስሎኝ መሬት ረገጥኩ፡፡ እግሬና ጆሮዬ ጋ በጣም ተጐድቼ ነበር። በተለይ የጆሮዬ አናቴን አናጋብኝና አዕምሮህ ላይ ችግር ይፈጥራል ሲሉኝ በሲቲ ስካን ታይቼ ምንም ችግር እንደ ሌለው ተነገረኝ፤ ግን ምቱ ሀይለኛ ስለነበር ለኮንሰርቱ መድረስ አልቻልኩም፡፡ ሀይለኛ ህመም ስለነበረው ማለቴ ነው፡፡
ምናልባት ዓውደ ዓመት ስለነበረ ትንሽ መጠጥ ቀማምሰህ ይሆን እንዴ?
አ…ይ… ነው ብለሽ ነው?
በተሠረዘው ኮንሠርት ብዙ ኪሳራ መድረሱን ሰምቻለሁ፡፡ እንዴት ነው?
ኪሣራው እኔ ነኝ፡፡ የእኔ መታመም ነው ኪሳራው፡፡ ባይሰረዝና ብጫወት ጥሩ ነበር፡፡ የእኔ ዘፈኖች ህፃናትን የሚያሳድጉ ናቸው፡፡ የህፃናትን አዕምሮ የሚያቆሽሽ ዘፈን አልሰራም፡፡ ህፃናትን አሳድጋለሁ፤ በዚህ ትርፋማ ነኝ፡፡ የእኔ መውደቅና መታመም እንጂ የብር ኪሳራ የለም፡፡
እንደሰማሁት ከሆነ ከኮንሰርቱ መሰረዝ ጋር በተያያዘ ወደ 700ሺህ ብር ኪሳራ ደርሷል፡፡ ይሄ እንደ ኪሳራ አይቆጠርም?
እሱ እኔን አያገባኝም …
የአንተ ብር የለበትም ማለት ነው?
እርግጥ የእኔም ብር አለበት፣ አዘጋጆቹ ከሚያወጡት ግማሹን አወጣለሁ፡፡ ቢጂአይም በርካታ ገንዘብ አውጥቷል፡፡ ነገር ግን ቢጂአይ ባወጣው ገንዘብ ሳይቆጭ፣ ፕሮሞሽናችንን በማድነቅ የዛሬውንም ኮንሠርት አጋራችን ሆኖ እየሠራ ነው፡፡ ከዛ በተረፈ ስለ ኪሣራ ስናወራ አሁንም ኪሣራው እኔ ነበርኩኝ፡፡ አሁን ጤናዬ ተመልሶ ድኛለሁ፤ ስለዚህ ምንም ኪሣራ የሚባል ነገር የለም፡፡
ቅድም ህፃናትን አሳድጋለሁ ብለኸኛል… እስቲ አብራራልኝ?
ምን ማለት ነው… ሁሌም የህፃናትን አዕምሮ በበጐ መልኩ የሚያንፁና የሚያሳድጉ ነገሮችን ነው የምዘፍነው፡፡ ዘፈኖቼ ለበጐ ስራ የተሠጡ፣ አስታራቂና አቀራራቢ ናቸው፡፡ የምስራች አብሣሪም ናቸው፡፡ እናም ይሄ ነገር ወደፊት ለአርት ሥራ የሚዘጋጁ ህፃናትን የሚያሳድግና ጥሩ አመለካከት እንዲይዙ ይረዳቸዋል ለማለት ነው፡፡ አየሽ ህፃናት ሁልጊዜ “አንጀቴን በላሽው” የሚል ዘፈን እየሠሙ ከሚያድጉ ስለ ፍቅር፣ ስለ ባህል፣ ስለ ጤናማ ግንኙነት እየሠሙ ቢያድጉ መልካም ነው። ለምሣሌ እኔ ያደግሁበት አስተዳደግና አሁን ልጆች እያደጉ ያሉበት መንገድ አንድ አይደለም ብዬ ነው፡፡
አለባበስህን የተመለከተ ጥያቄ ላንሳ፡፡ ጥለት ያላቸው ልብሶችን ራስህ ዲዛይን እያደረግህ እንጂ የተዘጋጁ ልብሶችን አትለብስም ይባላል፡፡ ይሄ ከምን የመጣ ነው? መቼ ነው የጀመርከው?
አሁንም የምታይው አለባበስ ያልሽው አይነት ነው፡፡ ከላይ ጀምሮ እስከማሸርጣቸው ልብሶች በሙሉ የአገሬ ልብሶች ናቸው፡፡ ይሄን መቼ ጀመርክ ላልሽው በጣም ቆይቷል ነው መልሴ፡፡ በጣም ረጅም ጊዜ ነው፡፡ አልበም ከማውጣቴ በፊት ማለቴ ነው፡፡
ነጭ የጠፍር ጫማና ነጭ ካልሲ ካልሆነ የትኛውንም አይነት ሽፍን ጫማ ቆዳም ይሁን ስኒከር አታደርግም። ቤትህ ውስጥ ጥልፍልፍ የጠፍር ጫማና ነጭ ካልሲ በገፍ ይገኛል ይባላል፡፡ ለምንድን ነው?
ደስ የሚለኝ እንደዛው ነው፤ ጐንበስ ስል ነጭ ሆኖ ሳየው ደስ ይለኛል፡፡ ሌሎቹን አይነት ጫማዎች አላውቃቸውም፤ ማወቅም አልፈልግም፡፡
የተለየ ምክንያት አለህ?
እኔ እንጃ! ይሄ ጫማ ልቤን ይዞብኛል (በዕለቱም ነጩን ጥልፍልፍ የጠፍር ጫማና ነጭ ካልሲ ተጫምቷል) ጐንበስ ስል ንፃቱ ለአይኔ ካልማረከኝ ትንሽ ጭንቅላቴን ይይዝብኛል፡፡ የእኔ ጭንቅላት ከተያዘ የሌላውም መያዙ አይቀርም፡፡ ስለዚህም ሌላውን አልደፍረውም፡፡
ስለ አዲሶቹና በአልበምህ ውስጥ ስላልተካተቱት አምስት ዘፈኖችህ እናውራ?
እንዴ? አምስት ዘፈን ዘፍኛለሁ እንዴ? እኔ እኮ ዘፈኖቼን አላውቃቸውም፡፡
“ኩሉን ማንኳለሽ”፣ “ታዲያስ አዲስ”፣ “ድግስ” የተሠኙትን ዘፈኖች ማለቴ ነው፡፡ እነዚህ አልበምህ ላይ የሉም…
ኦ! አዎ ልክ ነሽ “ዳጐስ”፣ “ድግስ”፣ “ታዲያስ አዲስ”፣ “ኩሉን ማንኳለሽ”፣ እና “ባቲ” የተሠኙ አዳዲስ እና የሚያማምሩ ሥራዎች ሠርቼያለሁ፡፡
ባህላዊና የሠርግ ዘፈኖችን ወደ ሬጌ ስልት ማምጣት አይከብድም?
በጣም ከባድ ነው፡፡ ነገር ግን የኔ ጭንቅላት ሙዚቃ ውስጥ ስለተነከረ ከጊዜ ወደ ጊዜ ቀለል እያለኝ መጥቷል። መጀመርያ አካባቢ ወደ ሬጌ ስልት መቀየር ትንሽ ያሰለቻል፤ ነገር ግን እኔ መሰልቸት ስለማላውቅ ስልቱን አገኘሁት፡፡ አሁን “እባክህ እንዲህ አይነት ሙዚቃ እፈልጋለሁ” ብዬ ልቤን እጠይቃለሁ፤ ልቤ ይሠጠኛል፡፡ በነገርሽ ላይ ሬጌ ላይ ግጥም ይከብዳል፡፡ ሬጌን ለመዝፈን ግጥም ነው ዋናው ነገር፡፡ ስለዚህ ግጥም ስፈልግ መንገድ ላይ ያገኘኋቸው ሀሳቦች ናቸው የሠርጉን የባህሉን ወደ ሬጌ እንዳመጣቸው ያደረገኝ፡፡ በፊት በፊት የሬጌ ግጥም የትግል ብቻ ይመስለኝ ነበር፡፡ እናም ብዙ ጊዜ ድርቅ ያሉ ግጥሞች ይሆኑብኛል፡፡ አሁን ግን ቀስ በቀስ እየተፍታታልኝ፣ በአጫጭር ግጥሞች ሀሣብ መግለፅ ጀምሬያለሁ፡፡ ይሄ እንግዲህ ከአስር ዓመት በኋላ የመጣ ነገር ነው፡፡
እንዳልከው ሬጌ አብዮተኛ የሙዚቃ ስልት ነው። ከደከሙበት ከጣሩበት ግን የፍቅርም የባህልም መግለጫ ይሆናል እያልክ ነው?
በሚገባ! እኔ አሁን ይህን እያደረግሁ ነው። ለምሣሌ “ታዲያስ አዲስ”፣ “ኩሉን ማን ኳለሽ” የተሠኙት ዘፈኖች ባህልንም ፍቅርንም የሚገልፁ ዘፈኖች ናቸው።
እስቲ ስለ ባህሪህ ንገረኝ… ቁጡ ነህ? ተጫዋች? ወይስ…
ስትቆጪኝ እቆጣለሁ፤ ስታጫውቺኝ እጫወታለሁ፡፡ እንደ አንቺ ተፈጥሮ የምጓዝ ነኝ፡፡ ተፈጥሮ እንደምትሆነው ነው የምሆነው ማለት ነው፡፡
እንደምሠማው ከሆነ ጃ ሉድ ትንሽ የባህሪ ችግር አለው፣ ከማናጀሮቹ ጋር እየተጣላ በተደጋጋሚ ማናጀር ቀይሯል፣ ከአቀናባሪው ከካሙዙና ከፕሮድዩሠሩ ታደለ ሮባም ጋር ሠላም አይደለም ይባላል፡፡ እውነት ነው?
ከታደለም ከካሙዙም ጋር አልተጣላንም፡፡ ባለፈው አሜሪካ ስሄድም ሸኝተውኛል፡፡ ታደለ ሮባ አሁንም ወዳጄ ነው፡፡ እንዳልኩሽ ባለፈው አሜሪካ ስሄድ ከካሙዙ ጋር መጥተው ሸኝተውኛል፡፡ ከአሜሪካ ስመለስ ግን ታደለ ሮባ ኢትዮጵያ ውስጥ አልነበረም፡፡ ካሙዙም ቢሆን አሁን ወደ አሜሪካ ሊሄድ ነው፡፡ እኔም በቅርቡ ስለምሄድ እዛው እንገናኛለን፡፡ ሁለተኛ አልበማችንን እዛ ልንጀምር ነው፡፡
ረዘም ላለ ጊዜ ልትቆይ ነዋ?
እኔ እመላለሣለሁ እንጂ ከአንድ ወር በላይ በየትኛውም አለም ከኢትዮጵያ ውጭ መቆየት አልችልም፡፡ አሁን መመላለስ እችላለሁ፤ ዓለም የኔ ናት፡፡ እንደ በፊቱ አይቸግረኝም፡፡ ከኢትዮጵያ ወጥቼ ረጅም ጊዜ ስቆይ ጤንነት አይሰማኝም። በክርስቲያኑ ፋሲካም፣ በሙስሊሙ የረመዳን ፆም ፍቺ (ኢድአልፈጥር) ጊዜም ከኢትዮጵያ ውጭ መሆን አልችልም፡፡ በጣም ደስ አይለኝም፤ ስለዚህ እመላለሳለሁ፡፡
እንደ በፊቱ አይቸግረኝም ስትል ምን ማለትህ ነው?
በፊት ከኢትዮጵያ ውጭ ዓለም ያለ አይመስለኝም ነበር፡፡ አሁን መሄድ መምጣት ለምጃለሁ ለማለት ነው። እርግጥ አሁን አሜሪካ የምሄደው ለስራ ስለምጠራ ነው እንጂ እዛ ለመኖርና ሌላው ስለሄደ መሄድ አለብኝ ብዬ አይደለም፡፡ በአጠቃላይ ከማናጀር ጋር ተጣላ፣ ከአቀናባሪ ተጋጨ፣ ፕሮዱዩሠሩን አኩርፎታል የሚባል ነገር የለም፡፡ ከሁሉም ጋር ሠላም ነኝ፣ እንደዛም ከሆነ ተበዳይ እኔ ነኝ፡፡ ነገር ግን አልበደሉኝም አልበደልኳቸውም፤ በእኔ ላይ የሚወራው ውሸት ነው፤ እንግዲህ አሉባልታ የሚወራበት ሌላ ጃ ሉድ ካለ አላውቅም፡፡
ከሬጌ ሙዚቃ እና ከህይወት ዘይቤያቸው (Style) ጋር ተያይዞ የሚነሳው የአደንዛዥ ዕፅ ጉዳይ ነው። አንዳንድ ሠዎች ጃ ሉድን ከዕፅ ጋር አገናኝተው ሲያነሱት ይደመጣል፣ የባለፈውን ኮንሠርት ያሠረዘህን አወዳደቅም ሀሺሽ ከመውሠድ ጋር ያገናኙት አልጠፉም፡፡ በዚህ ጉዳይ ምን ትላለህ?
በፈጠረሽ ተይው፡፡ ምንም ነገር የለም! ይህንን ነገር ተይው፡፡ አሁን ህዝቡ በዚህ መልኩ እኔን መቃኘት የለበትም፡፡ እውነት ለመናገር ይህንን ነገር ላድርገው ብል አደርገዋለሁ፣ መብቴ ነው፡፡ ነገር ግን ምንም ነገር የለም፡፡ እውነቴን ነው የምልሽ የለሁበትም!
ሰዎች ቀጠን ማለትህንና የኪሎህን ነገር እያዩ ምግብ በደንብ አይበላም፣ ከምግብ ጋር ያለው ዝምድና የጠበቀ አይደለም ይላሉ፡፡ ለምንድን ነው በደንብ የማትመገበው?
እየውልሽ… ሰዎች ሁሉ ምግብ አይመገብም እያሉ ብዙ ሳልመገብ ቀረሁ፡፡ ይመገባል ቢሉኝ ኖሮ ብዙ እመገብ ነበር፡፡ ምክንያቱም “እሹ ይሰጣችኋል” ነው የሚለው መፅሀፉ፡፡ አሁን ብዙ ይመገባል እያሉ ቢያበረታቱኝና ብመገብ ደስ ይለኛል፡፡
ከ”መሀሪ ብራዘርስ” ባንድ ጋር ምን ያህል ተጣጥማችኋል?
“መሀሪ ብራዘርስ” በጣም ፍቅር የሆኑና ለሙያው ራሣቸውን የሠጡ ወጣቶች ናቸው፡፡ አሜሪካም፣ አውሮፓም በአጠቃላይ እዚህም ያለውን ኮንሠርት ከእነሱ ጋር ብሰራ በጣም ደስ ይለኛል፡፡ ለእኔ በጣም ተስማምተውኛል፡፡ እርግጥ አሜሪካ “ዛዮን” ባንዶች አሉ፡፡ እዚህ ያለውን ከመሀሪ ብራዘርስ ጋር ነው የምሠራው፡፡ አውሮፓና አፍሪካ አገር ካሉ ፕሮሞተሮች ጋር ትንሽ ጉዳዮች አሉኝ፡፡ እነሱን ካስማማሁኝ “መሀሪ ብራዘርስ” ከእኔ ጋር ለበርካታ ጊዜያት ይቆያሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡ በጣም ጥሩ ልጆች ናቸው፤ ፍቅር የሆኑ ወንድማማቾች ናቸው። እንዲህ አይነት ወንድማማችነት ውስጥ ተካትቼ ለረጅም ጊዜ ብኖር ደስ ይለኛል፡፡

 

Published in ጥበብ

ትርጉም እያዛባ፣ቃል እያናናቀ፣
ፍቺ እያጣረሰ፤
ከበሽታ ሁሉ የደሃ ኩርፊያ ነው
ሃገር ያፈረሰ።
እናንተ ብልሆች!
ተስፋ−ተስፋ የሚሸት እቅድ ስታቅዱ፣
ንቁ−ፍኩ እንዲሆን የለውጥ መንገዱ፤
‘ካኮረፈ ደሃ’ ሃሳብ አትውሰዱ!

የለቅሶ ቤት አዝማች
ተዝካር፣
እዝን፣
ድንኳን፣
ንፍሮ፣
ሰልስት፤
12፣ 40፣ 80፣ ሙት−ዓመት፤
“ጐጂ ነው!” አትበሉን አቦ እናልቅስበት!
እናውቃለን እኮ!
አዛኞች፣ አጽናኞች በሞሉባት አምባ፤
‘ግማሽ ሳቅ’ ማለት ነው ሁሉ ያየው ዕንባ።

Published in የግጥም ጥግ
Page 7 of 17