የጀግና ሰው መልኩ ሁለት ብቻ ነው፤ አንድ ፊት መስዋዕት በአንድ ፊት ድሉ ነው፤ የሁሉም ማሰሪያ ማተቡ ብቻ ነው፡፡ (“የአሲምባ ፍቅር” ገፅ 140) ካህሳይ አብርሃ ወይም በበረሀ ስሙ አማኑኤል ተብሎ ይጠራል፡፡ መስከረም 27ቀን 1968 ዓም የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ሰራዊትን ለመቀላቀል ወደ ትግል ወጣ፡፡ ሰኔ 27ቀን 1968 ዓም ወልዲያ ለተልዕኮ የወጣ የሠራዊቱ ቡድን ወደ አሲምባ በተመለሠበት ዕለት በተፈጠረ የጦርነት አጋጣሚ ከይመር ንጉሴ ጋር ተገናኘ፡፡

በ1970 በኤርትራ አድርጎ ሱዳን በመግባት ከሠራዊቱ ተለየ፡፡ ኑሮውም በአሜሪካ ሆነ፡፡ የደርግ አገዛዝ ሲገረሰስ ይመር ንጉሴን ለማግኘት እንዲሁም የመጀመሪያ የሴት ፍቅረኛው የተሠዋችበትን ቦታ ለማየት ወደ ኢትዮጵያ መጣ። በሰራዊቱ ውስጥ ስላሳለፈው የትግል ህይወት የሚተርክ “የአሲምባ ፍቅር” የተሰኘ መፅሀፍ ባለፈው ቅዳሜ የቀድሞ የኢህአፓ አባላትና ሌሎች እንግዶች በተገኙበት አስመርቋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ በአሜሪካ ከሚኖረውና በፋርማሲ ባለሙያነት ከተሰማራው ካህሳይ አብርሃ ጋር ስለ መፅሀፉ እና የትግል ህይወቱ አነጋግራዋለች፡፡

                                                    ***

በየትኛው ስም ልጠቀም---- አማኑኤል በሚለው ወይስ በበረሀ ስምህ ካህሳይ? በፈለግሽው መጠቀም ትችያለሽ፡፡ ወደ አሲምባ የገባህበትን የመጀመሪያዎቹን ቀናት እንዴት ታስታውሳቸዋለህ? ስሜቱን ልገልፀው አልችልም፡፡ ለመብት ከሚታገል ድርጅት ጋር መቀላቀል ደስታ ፈጥሮብኝ ነበር፡፡ ኑሮው ውጣ ውረድ ያለበት መሆኑ አልከበደህም? ረሀቡ፣ ጥማቱ እና ውጣ ውረዱ ያለ መሆኑን ገምቼ ስለገባሁበት እንቅፋት አልሆነብኝም፡፡ የታጠቁትን መሳሪያ ሳይ ደግሞ በጣም ደስ አለኝ። እዛ ያሉትን ጓዶች ሳያቸው የበለጠ ተደሰትኩ፡፡ በጣም አዋቂ ሰዎች ነበሩ፡፡ ከሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢ የመጡ፡፡ የኢህአፓ አባል የሆንከው ቆይተህ ነው፡፡ ለረጅም ጊዜ የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ሠራዊት (ኢህአሠ) አባል ነበርክ፡፡ ስለፓርቲው ምን ያህል እውቀት ነበረህ? ፓርቲው የበላይ አካል እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ የፓርቲ አባል ባልሆንም የሚደረጉትን ነገሮች በሙሉ አውቅ ነበር፡፡

ለምሳሌ የፓርቲው አባሎች ስብሰባ ሲያደርጉ ለፀጥታ ጉዳይና ለደህንነት በሚል መሪዎች ይነግሩናል፡፡ ስለዚህ ኮሚሳሩ “እገሌ እገሌን ይዘን እንሄዳለን” ካለኝ የፓርቲ ስብሰባ እንዳለ እናውቃለን ማለት ነው፡፡ የሆነ መመሪያ በሚወጣበት ጊዜ በመጀመሪያ የፓርቲ አባሎች ይወያዩበታል፤ ከዛ ወደ ሠራዊቱ ይመጣል፡፡ የፓርቲ አባል ስሆን በህይወት እቆያለሁ የሚል ሀሳብ አልነበረኝም፡፡ በማንኛውም ወቅት ግዳጄን ስወጣ ህይወቴ ሊያልፍ እንደሚችል ነበር የማምነው፡፡ እስቲ ይመር ንጉሴ ከተባለው የገበሬ ሚሊሻ ጋር የተገናኛችሁበትን አስገራሚ ገጠመኝና ከዛ በኋላ የሆነውን ነገር ንገረኝ … ወሎ ግዳጅ ወጥተን ጉራወርቄ በምትባል ቦታ እየሄድን የሁካታ ድምፅ ሰማን፡፡ የገበሬ ታጣቂ ሚሊሽያዎች ከኋላችን እየተከተሉን ነበር፡፡ አጠገባችን ሲደርሱ ተኩስ ከፈቱ፡፡ አንዳንድ ጓዶች ጥይት ጨርሰዋል፡፡ አንዱ በመጥረቢያ ተመትቶ ወድቋል፤ ሌላው በጩቤ ተወግቷል፡፡

ሁኔታዎች ከቁጥጥራችን ውጪ ሆነዋል፡፡ በዚህ መሀል ያነጣጠርኩበትን ገበሬ ያለምንም ጥቅም እንደምገድለው እርግጠኛ ነበርኩ። በዚያ ሁኔታ ውስጥ ነፍስ ማጥፋት ዋጋ እንደሌለው ተሰማኝ፡፡ በመተኮስና ባለመተኮስ መሀል ሳመነታ ገበሬው ሰፈረብኝ፣ ተያያዝን ወደቅን፡፡ “ጥይት አልጨረስክም፤ ለምን ተኩሰህ አልገደልከኝም” ሲለኝ “እንኳን አልገደልኩህ” አልኩት፡፡ ምን መለሰልህ? በጣም ገርሞት “ምን ማለትህ ነው” አለኝ፡፡ “አንተ ምናልባት የምታስተዳድራቸው ብዙ ሰዎች ሊኖሩ ይችላሉ፣ እኔ የለኝም፡፡ ብትገድለኝ አንድ ብቻዬን ነኝ” ስለው በተኛሁበት በያዘው ገመድ እጆቼን ማሰሩን ተወው፡፡ የሞቱትን ጓዶቻችንን ከቀበርን በኋላ፣ ጠመንጃውን አውርዶ ወደ ሰማይ እየተኮሰ ወደእኔ መጣ፡፡ “ይህን ሰው አላስይዝም፤ መሄድ ወደሚፈልግበት እሸኘዋለሁ” ብሎ ወደቤቱ ወሰደኝ፡፡ ከዛስ? የመጀመሪያው ሌሊት እንቅልፍ የሚባል በአይኔ አልዞረም፡፡

ምክንያቱም ጠዋት ምን ሊፈጠር እንደሚችል እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ ይገድለኛል? ያስረኛል? አሳልፎ ይሰጠኛል የማውቀው ነገር የለም። ስለዚህ ጠዋት ማምለጥ የምችልበትን ሁኔታ እያሰላሰልኩ ነበር፡፡ ነገር ግን ወዲያው እሱ እኔን ይዞ ሲመጣ ፈጥኖ ደራሽ መጥቶ “ይመር ንጉሴ” እየተባለ ሲጠራ ሰምቻለሁ፡፡ እሱ ግን “ምንም አትሆንም አሳልፌ አልሰጥህም፤ ወደዚህ የሚመጡና የምንታኮስ ከሆነ ወደ ደኑ ማምለጥ ትችላለህ፡፡ እኔ በህይወት ካለሁ መጥቼ እፈልግሀለሁ” ሲለኝ እሱን ከማመን ውጪ ምንም ምርጫ እንደሌለኝ አወቅሁኝ፡፡ በዚህ ወቅት ምን ተሰማህ? እኔና ይመር በህይወት ተቀያይረናል፡፡ እሱን እኔ አልገደልኩትም፤ እሱም በተራው የእኔን ህይወት አትርፏል፡፡ ከዛ ወደ ሚስቱ ዘመዶች አገር ወስዶኝ ተመልሼ አሲምባ ገባሁ፡፡ አሲምባን ስናስብ የሚመጣብን የጦርነት ታሪክ ነው፡፡ መፅሀፍህ “የአሲምባ ፍቅር” ይላል፡፡

እስቲ ስለ አሲምባ እና ፍቅር ግንኙነት ንገረኝ? አሲምባ የኢህአሰ የመጀመሪያው ቤዝ ነው። አሲምባ ላይ ብዙ ነገሮች ተካሂደዋል፡፡ ሰዎች ተገድለውበታል፡፡ ግን እኔ የማየው ከዛ በላይ ነው። ምክንያቱም የጓዶች ፍቅርና መተሳሰብ … ከብዙ የተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች የተውጣጡ ግን የአንድ ቤተሰብ ያህል የሚተሳሰቡና የሚዋደዱ ነበሩ። ሠራዊቱ ከህዝቡ ጋር ህዝቡም ከሠራዊቱ ጋር ያለውን ፍቅር ያሳያል፡፡ ህዝቡ ባይፈቅድ ኖሮ እዛ መኖር አንችልም ነበር፡፡ ሌላው የአገሩ ፍቅር ነው። ጋራው፣ ሸንተረሩ፣ ወንዙ ይናፍቃል፡፡ ትግራይ፣ ወሎ፣ በጌምድር ሁሉም የሚናፈቅ ፍቅር አላቸው፡፡ የመጀመሪያ የሴት ፍቅረኛዬ እና ጓዴ የድላይ ፍቅር አለ፡፡ አንተ የፍቅር ጓደኝነት በጀመርክበት ጊዜ ፓርቲው ያንን ይፈቅድ ነበር? አይፈቅድም እንደዚህ ዓይነት ግንኙነት ተፈጽሞ ቢገኝ እርምጃው ምንድነው? በህገ ደንቡ መሠረት መባረር ነው፡፡ ግን ፍቅረኞች ነበርን እንጂ ወሲብ አልፈፀምንም፡፡ ስለ ኃይማኖት አቋምህ ስትጠየቅ የተሰማህ ስሜት ምን ነበር? ኃይማኖት ከሌለኝ ኮምኒስት አይደለህም የምባል ወይም የሚመልሱኝ መስሎኝ ስጋት ገብቶኝ ነበር ግን እውነቱን ነግሬያቸዋለሁ፡፡ እስቲ ስለ በረሀ ምግቦች ንገረኝ? ምን ነበር የምትበሉት? ቁርስ የሚባል ነገር የለም፡፡ ለምሳ ለእራትም የሚባል ራሸን የለም፡፡ ያገኘነውን ነው የምንበላው።

ዳቦም ይሁን ቂጣ ወይም እንጀራ ህዝብ የሰጠሽን ትበያለሽ፤ ህዝብ ካልሰጠሽ ደግሞ የተገኘውን ነው የምትበይው፡፡ በለስም ቢሆን … ካልተገኘ ደግሞ ውሀ ጠጥተሽ ታድሪያለሽ፡፡ ውሀም የማይገኝበት ጊዜ አለ። ያንንም መቻል ነው፡፡ አንድ ጊዜ ወደ አርባያ በለሳ ስንሄድ ውሀ በጣም ጠማን፡፡ አንድ ወንዝ አገኘን፤ ውሀው በጣም ቆሻሻ ነበር፤ ግን ትንሽ መጐንጨት ነበረብን፡፡ በነጠላ ትሎቹን እያጠለልን ትንሽ ተንሽ ቀምሰን ሄደናል፡፡ ሽንት የሚጠጡም ነበሩ፡፡ በመፅሃፍህ ውስጥ ፀጋዬ ገብረመድህን (ደብተራው) “ቅማል መቅመል ይወዳል” ብለሀል፡፡ እስቲ ስለሱ ንገረኝ…. በየጊዜው ገላ መታጠብ እና ልብስ ማጠብ አይቻልም፡፡ አኗኗራችን የትግል ነው፤ ከቦታ ቦታ ነው የምንሄደው፡፡ ጊዜ ስናገኝ እንቀማመል ነበር። በተለይ ደብተራው መቅመል ይወዳል፡፡ ልጆች ስለነበርን በቅማል ስንሰቃይ በጣም ይጨንቀው ነበር፡፡ ቅማላችንን አራግፎ ሲሰደን በጣም ነበር የሚደሰተው። እኛ ደግሞ እሱን እንቀምለው ነበር። አንድ ጊዜ በኤርትራ በኩል የመጣ መድሃኒት ነበር፤ ዱቄት ነው፡፡ በውሀ በጥብጠን ልብሳችንን እንነክረዋለን፤ ከዛ እናሰጣዋለን፤ ቅማሎች ይራገፋሉ። አንዳንዴ ለፀጉራችንም እንጠቀምበት ነበር፡፡

ግን በጣም አደገኛ ነው፤ አንዳንዶች ራሳቸውን ይስቱ ነበር፡፡ ምክንያቱም መጠኑን አናውቀውም ነበር፡፡ ሰራዊቱ የሴቶች አያያዝ ላይ እንዴት ነበር? በእኩልነት ላይ የተመሰረተ ነበር፡፡ የሴቶች ጭቆና ድርብርብ መሆኑን ያምን ነበር፡፡ የመደብ እና የፆታ ችግር እንዳለ ያምናል፡፡ ከመጀመሪያ ፍቅረኛህ ከድላይ ጋር እቃ እንድታመጣ አብራችሁ ሄዳችሁ ነበር፡፡ እስቲ ስለሱ ደግሞ … ጓዶች ሱሪህን አውልቀህ ስጣት አሉኝ፡፡ ያኔ የሚቀልዱ ነበር የመሰለኝ፡፡ “ቶሎ በል ጊዜ ስለሌለ ቶሎ አውልቀህ ስጣት” ስባል ነው ያመንኩት፡፡ ትንሽ ዞር ብዬ ነጠላዬን አገለደምኩና ሱሪዬን አውልቄ ሰጠኋት፡፡ ያኔ ሱሪዋ ቆሽሾ ይሆናል ብዬ ነበር ያሰብኩት፡፡ ወደ ማታ ደግሞ “ይዘሀት ወደ ነበለት ትገባለህ፤ የምትፈልገውን እቃ ይዛ ትመለሳለች” ሲሉኝ ለድርጅቱ ስራ አብሪያት እንደምሄድ ነበር የጠረጠርኩት፡፡ እሷን ስጠይቃት ግን ሞዴስ ላመጣ ነው አለችኝ፡፡ ምን እንደሆነ ስጠይቃት ብትነግረኝም አልገባኝም፡፡

በመንገድ ላይ ስኮረኩራት ስኮረኩራት ነው ምን እንደሆነ የነገረችኝ፡፡ ፍቅረኛህ ድላይ በተደጋጋሚ ውሳኔህን እንድታሳውቃት ታስጠነቅቅህ ነበር፡፡ ሰራዊቱን ትተህ ወደ ሱዳን ለመውጣት ስታስብ ለመንገር ባትችል እንኳን ለምን መልዕክት አልላክባትም? ሱዳን ሆኜ ተስፋይ ኢዲዩ ደብዳቤ ላድርስልህ ቢለኝም የምልከው በነሱ ከሆነ ያነቡታል፤ ስለዚህ የግል ሚስጥር የሚባል ነገር የለም፤ ለዚህ ነው ደብዳቤውን ያልላኩት፡፡ አሲምባ የሠራዊቱ ፍርድ ቤት ነበር፡፡ አንተም ተከሰህ ለፍርድ ቀርበህ እንደነበር በመፅሃፉ ገልፀሃል። የፍርድ ቤቱ ውሳኔ ፍትሀዊ ነው የሚል አዝማሚያ በፅሁፍህ ላይ ይንፀባረቃል፡፡ እውነት ፍትሀዊ ነበር ትላለህ? ለኔ በጣም ፍትሃዊ ነው፡፡ እኔ ከስሼም ተከስሼም ስለማላውቅ አማካሪ ያስፈልገዋል ተባልኩ፡፡ በዚህ ምክንያት ነው ሰላማዊት ጠበቃዬ የሆነችው፡፡ መከሰሴን ተገቢ ነው ባልልም ውሳኔው ግን ጥሩ ነበር። ፀሎተ ህዝቅያስ በፍርድ ቤት ውሳኔ ነው የተገደለው? መፅሐፍህ ላይ “ፀሎተን ደጀኔ ገደለው፣ ደጀኔን ዳዊት ገደለው፣ ደብተራው ወደ ላይ እየተኮሰ መጣ” ብለህ ነው የገለፅከው፡፡ ምንድን ነበር የሆነው? ያየሁትን ብቻ ነው የምናገረው፡፡ ፀሎተ ገና ሳይሞት ነው የደረስኩት፤ ደጀኔ ሞቶ ነበር፡፡ ይሄ የፍርድ ቤት ውሳኔ አይደለም፡፡

በዛን ጊዜ ማንኛውም የአመራር አባል ለደህንነቱ ሲባል የሚሄድበትን ይነግረናል፡፡ ጠዋት ደብተራው መጣና “ደጀኔና ፀሎተ ወደ ወንዝ ለመታጠብ ሄደዋል፤ ጥበቃ እንዲደረግላቸው” ሲለኝ የተባለው ተደረገ፡፡ በተለይ ፀሎተ የአመራር አባል ስለሆነ ጥበቃው ጠንከር ይላል፡፡ ከዛ ደብተራው ትንሽ ቆይቶ ተመለሰና “እኔና ዳዊት ይህ ቦታ ስለጠበበን ፊትለፊት ካለው ጋራ ቤት እናያለን፤ ስለዚህ ጥበቃ ይደረግ” አለ፤ ያንን አደረግን። ወድያው የሁለት አውቶማቲክ መሳሪያ ተኩስ ሰማን፡፡ መጀመሪያ እኔ ወደ ወንዙ ስደርስ ደብተራው ወጥቶ ሽጉጥ ወደሰማይ ይተኩሳል፡፡ እርዳታ ፈልጐ ይመስለኛል፡፡ እኔ ከደብተራው በስተቀር ሁሉም የተገደሉ ነበር የመሰለኝ ፡፡ ደብተራውን ምን ተፈጠረ ብዬ ስጠይቀው “ደጀኔ ፀሎተን ገደለው፤ እኛ ደግሞ ደጀኔን ገደልነው” አለኝ፡፡ ደጀኔ ሞቷል፤ ፀሎተ አልሞተም ነበር፡፡ ዳዊት ጭንቅላቱን ይዞ ሲያለቅስ ነበር፡፡ ፀሎተን ወደ ጥላ ወሰድነው፤ ከዛም ብዙ ሳይቆይ ሞተ፡፡ የዕበዮ፤ የኢህአሰ ሰራዊት ውቅሮ ላይ ባደረገው ውጊያ ነው የተገደለው፡፡ ከሱ ጋር ያለውን ተያያዥ ታሪክ ንገረኝ… የዕበዮ የውቅሮ ልጅ ነው፡፡

ስለዚህ ውቅሮ በሚደረገው ውጊያ እንዳይገባ ተወስኖ አይሆንም ብሎ ተከራክሮ ነበር ወደ ውጊያው የገባው፡፡ በውጊያው ከተሰዋ በኋላ በህይወት የተረፍነው እሱን ስንቀብር ሌሎቹ ጓዶች “አንገቱ ይቆረጥና ይቀበር፤ ምክንያቱም ደርግ የእሱ አስከሬን መሆኑን ከለየ መንገድ ላይ ያወጣዋል” ሲሉኝ “አይኔ እያየ አንገቱን አይቆረጥም” ብዬ ሳይቆረጥ ተቀበረ፡፡ እኔ ሠራዊቱን ትቼ ሱዳን ከገባሁ በኋላ ደርግ በማግስቱ አስከሬኑን ስለለየው ውቅሮ ከተማ መንገድ ላይ አስከሬኑን በመዘርጋቱ፣ እናቱም ያንን አይታ የአዕምሮ ህመምተኛ እንደሆነች ሰማሁ፡፡ ዛሬ ላይ ሳስበው ተቆርጦ ቢሆን ኖሮ እናቱ ትድን ነበር እላለሁ፡፡ ያን ጊዜ ግን የምወደውን ሰው አንገት ቆርጦ ለመውሰድ ህሊናዬ አልፈቀደልኝም፡፡ በበጌ ምድር፣ በባሕር ዳር በየከተማው የነበረውን የኢህአፓ እንቅስቃሴ በቅርበት ታውቁ ነበር? በረሃ በወጡት የፓርቲው ተወካዮች በኩል የምንሰማው መረጃ እንጂ ሌላ እውቀት የለም፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጋር ስትገናኙ እንዴት ነበር? የተገናኘው በ1968 ዓ.ም ነው፡፡ ከራዛ ጦርነት በኋላ የተገኘውን መሳሪያ ለመውሰድ ኤርትራ ውስጥ መነኩሲቶ የምትባል ቦታ ሄድን፡፡ አቶ መለስን አይተነው፤ ስለሱ ሰምተንም አናውቅም ነበር፡፡ እሱ የሆነ መልዕክት ይዞ የመጣ ይመስለኛል፡፡ ለሊቱን በመደዳ ተኝተን አሳለፍን፡፡ በቆይታችን ስለነበረን ልዩነቶች ተነጋግረናል፡፡ የሀሳብ ልዩነት ላይ መስማማት ስላልቻልን “ብሬይን ወሽድ ስለሆናችሁ እናንተን ማሳመን አይቻልም” አለን፡፡

ቃሉን ለመጀመሪያ ጊዜ ስለሰማሁት ፃፍኩትና ወደ ቦታችን ስንመለስ፣ መለስ ያለንን ነገርኳቸውና ምን ማለት እንደሆነ አስረዱኝ፡፡ ከህወሓት እና ከኢህአፓ ህዝቡ የቱን እንደሚመርጥ ሪፈረንደም አድርጋችሁ ነበር፡፡ እስቲ ምንድነው የሆነው? በወቅቱ የአንድ መንደር ህዝብ አስተዳዳሪው የቱ እንደሚሆን ይመርጥ ነበር፡፡ ከሁለቱ ድርጅቶች በየቱ መተዳደር ትፈልጋላችሁ ይባልና ውሳኔው ተግባራዊ ይደረጋል፡፡ ወያኔ ካለ እኛ እንለቃለን፤ ኢህአፓ ካሉ እነሱ ይለቃሉ፡፡ ህዝቡ ተወካዩን እንዲመርጥ እናደርጋለን፡፡ ታድያ ሁኔታዎች ለምን ተበላሹ? በሁለቱ ድርጅቶች መካከል የተፈጠረው ነገር በኔ ደረጃ የሚገለፅ አይደለም፤ እኔ ተራ ታጋይ ነበርኩ፡፡ ከበለሳው ቡድን በኋላ ኢህዴን/ብአዴን ከሆኑት ማንን ታውቃለህ? ያኔ አብረውን ከነበሩ ሰዎች እንደሰማሁት አርባፀጓር ላይ አቶ በረከት ስምኦን አጠገቤ እንደነበሩ ነግረውኛል፡፡ ግን አንተዋወቅም፡፡ አቶ በረከትም ከቤጌምድር ጋንታ መጥቶ ነበር፡፡ ከደብተራው ጋር ከነበራችሁ ፍቅር የተነሳ ስትለያዩ ማስታወሻ ስጠኝ ብለኸው ለማስታወሻነት መሳሪያችሁን ተለዋውጣችኋል፡፡ የደብተራው ማስታወሻ መሳሪያ የት ገባች? ከደብተራው ጋር ለየት ያለ ፍቅር ነበረን፡፡ በኔ ላይ ጥሩ እምነት ነበረው፡፡

ስለ አማኑኤል ጥሩ እንጂ መጥፎ ነገር አትንገሩኝ ይል እንደነበር አሁን በህይወት ያሉ አመራሮች ይነግሩኛል፡፡ ስንለያይ ብረት ተለዋወጥን፡፡ ወደ ሱዳን ስሄድ በኤርትራ በኩል ስለሆነ ለኤርትራ ድርጅት አስረከብኳት፡፡ ሳስረክባት እውነቴን ነው እሱንም ያስረከብኩት ነው የመሰለኝ፡፡ ኢህአፓ እና ኢህአሠ የተቆራኙ ወይም የሚናበቡ አይመስሉም፡፡ ወታደራዊ ግዳጆቹ የተበጣጠሱ ናቸው፡፡ ስለዚህ ጉዳይ ምን ትላለህ? እኔ በማውቀው ደረጃ ያንቺን ጥያቄ መመለስ ይከብደኛል፡፡ እኛ ዛሬ እዚህ ትሄዳላችሁ ስንባል እንሄዳለን፤ ውጊያ ታካሂዳላችሁ ሲባል እንፈፅማለን። ፓርቲው ሠራዊቱን ያዛል፤ ሠራዊቱ ይፈፅማል፤ በየክፍሉ የፓርቲ ወኪሎች አሉ፡፡ በሠራዊቱ ውስጥ የነበረው የተማሩና ያልተማሩ አባላትን ልዩነት ንገረኝ? እኛ የታዘዝነውን እንፈፅማለን፡፡

አንዳንድ የተማሩት እኛን “የአመራር ቡችሎች” እና “ክሊኮች” ይሉናል፡፡ እኛ ስለፓርቲው ጠልቀን አናውቅም፤ እነሱ ስለፓርቲው ድክመትና መፈረካከስ ያውቃሉ፤ በዚህ መሀል መናበብ የለም፡፡ ያኔ እነሱ ተስፋ መቁረጥ ውስጥ ናቸው፤ እኛ ደግሞ ለምን የታዘዙትን አይፈፅሙም እንላለን፡፡ እኛ ስላልተማርን ንቀውን ሳይሆን ውስጣችን የተለያየ ነገር ስለነበር ነው፤ በአቅምም እንድናድግ ጥረት ይደረግ ነበር፡፡ ለምሳሌ ጓድ ሽፈራው “The military Tactic of the Vietnamese Revolution” የሚል መፅሐፍ አስነብቦናል፡፡ ኢህአፓ/ኢህአሠ ለምን ፈረሰ? ብዙ ብቃት ያላቸው ለመስዋእትነት ዝግጁ የሆነ ሠራዊት ነበረው፡፡ ድርጅቱ ለምን ፈረሰ በኔ አቅም አይመለስም፡፡ ልዩነቶች እንደነበሩ እንሰማ ነበር፡፡ እኛ በይፋ የተነገረን በ1970 ቢሆንም ችግሩ ከ1968 ጀምሮ የነበረ ነው፡፡ ብርሃነመስቀል ከድርጅቱ ወጥቷል ይባል ነበር፡፡ ያንን የፓርቲ አባሎች ያውቃሉ፡፡

እኛ ግን በሀሜት ደረጃ እንጂ በይፋ አልተነገረንም፡፡ ድርጅቱ እየተከፋፈለ አንጃ ተብለው ታስረው የተገደሉ አሉ። በጣም የምንወዳቸውና የምናከብራቸው መዝሙር፣ በሽር፣ ታሪኩ የተባሉ እና ሌሎችም ተገደሉ፡፡ ብዙ ጓዶች በዚህ ላይ ቅሬታ ነበራቸው፡፡ ከኤርትራና ከወያኔ ጋር የነበረን ግንኙነት መሻከር ተደማምረው ይመስለኛል ለመፍረስ የበቃው፡፡ “የአሲምባ ፍቅር” … ይቅርታ ጠይቀን አስቆምናቸውና “እዚህ አካባቢ የሚኖር ሰው ብጠይቃችሁ ታውቃላችሁ?” አልናቸው፡፡ አንደኛው ሰውዬ “መሃመድ እባላለሁ፤ እዚሁ አካባቢ ነው ሀገሬ ፣እዚህ ወጣ ብሎ ይሄንን ጋራ ተሻግራችሁ ነው፡፡ ማንን ፈልጋችሁ ነው? ስሙን ታውቃላችሁ?” አሉን፡፡ “ይመር ንጉሴ የሚባል ሰው” አልኳቸው “ይመር ንጉሴ? ወይ ወንድሜን!” ብለው ጭንቅላታቸውን ይዘው ማልቀስ ጀመሩ፡፡ ልቤ ስንጥቅ አለ፡፡

የሆነውን መጠየቅ አስፈላጊ አልነበረም፤ አውቄዋለሁ፡፡ እውነቱን መቀበል ግን አልፈለግኩም፡፡ ለመናገር መዘጋጀቴን ሳላውቀው ከአፌ ምነው? የሚል ቃል ሲወጣ በጆሮዎቼ ተሰማኝ። “ይመር ንጉሴ እኮ ሞቷል!” አሉ፡፡ “እንዴት ሆኖ?” “በቃ እንዴት እንደሆነ አላወቅንም፤” የወያኔ ታጋዳዮችና በርካታ መሪዎች አውቅ ነበር፤ ብዙዎቹን በአካል ሌሎቹን ደግሞ በዝናና በወሬ ደረጃ ስማቸውን ሰምቻለሁ፣መለስን ግን ያየሁትም ሆነ ስሙን የሰማሁት ለመጀመሪያ ጊዜ ነው፡፡ መለስ የለበሰው የዘማቾች ካኪ ዩኒፎርም ሲሆን አንድ ቦርሳ ሙሉ መፅሃፍ ይዟል፡፡ ሰውነቱ ጠንካራ፣ ከመካከለኛ ሰው ትንሽ አጠር ያለ ቁመት ያለው፣ ክብ ፊትና ንቁ ዓይኖች ያለው ሰው ነው፡፡ መለስ ጨዋታና ቀልድ የሚያውቅ፣ ሃለኛ ተከራካሪ፣ በውይይት ጊዜ ፊቱን ቅጭም የሚያደርግና የሚመሰጥ እንደሆነ በዛን ቀን ቆይታችን አስተውያለሁ፡፡…የምንከራከረው እኔና አስመሮም ከአንድ ወገን፣ መለስ ደግሞ ብቻውን ስለነበር ውይታችን አድካሚ ሳይሆንበት አልቀረም። እርሱ ግን እንዲህ በቀላሉ ደክሞት የሚተው ሰው አልነበረምና እኛን ለማሳመን ብዙ ደከመ።

በመጨረሻም ከሀሳቡ መደጋገም በቀር አዲስ ነገር እያለቀብን ሲመጣ፣ “ብሬይን ወሸድ(brain washed) ስለሆናችሁ፣ እናንተን ማሳመን አይቻልም” አለ፡፡ ጸጋዬ ደብተራውን በጣም ስለምወደው “አሁን ጎንደር ከሄድኩ ላንገናኝ እንችላለንና አንተን ማስታወሻ የሚሆነኝ አንድ ነገር ስጠኝ” አልኩት፡፡ እሱም ሳቅ አለና ትንሽ ካሰበ በኋላ “እንካ ጠመንጃዬን ልቀይርህና ማስታወሻ ይሆንልሃል” ብሎ ሰጠኝ፡፡ የእርሱን ወስጄ የእኔን ሰጠሁትና ተቃቅፈን ተሳሳምን፡፡ ሁለቱም የክላሽን ኮቭ ጠመንጃዎች ነበሩ፤ምንም ልዩነት የላቸውም፡፡ ቢያንስ አንዳንዴ ጠመንጃዬን ሳይ ግን እሱን ያስታውሰኛል ብዬ በጣም ደስ አለኝ፡፡

… በጣም ግራ ገባኝ “ከሴት አስተማሪዎች የምትቀበይው ወይም ደግሞ የምታመጪው ምን እቃ ነው?” ብዬ እንደገና ስጠይቃት ሳቀች፡፡ “አንተ አታውቀውም፣ የሴት እቃ ነው፣ አማኑኤል” አለችና እንደገና አከታትላ “አማኑኤል እኔ እኮ አሞኛል፡፡ ቀኑን በሙሉ ያንተን ልብስ ለብሼ እንደዋልኩ ታውቅ የለ፡፡ የእኔ ሱሪ ተበላሽቶ ስለነበር ለማጠብ ነበር የአንተን ለብሼ ወደ ወንዝ የወረድኩት” ብትለኝም ችግሯን በትክክል አልተረዳሁትም፡፡ “ታዲያ ምንድን ነው የምናመጣው?” “እቃው ሞዴስ ይባላል” አለችኝ፡፡ “ሞዴስ ምንድነው?” “ሞዴስ ሴቶች ብቻ የሚጠቀሙበት የሴት እቃ ነው፡፡ ወንዶች ብዙም አታውቁትም” አለችና ለአፍታ ያህል ስታስብ ቆየች፡፡ “ወንዶች እኮ እንደዚህ ዓይነት ነገር ስለማታውቁ ታድላችኋል” በድምጿ ውስጥ ሐዘን ተሰማኝ፤ ችግሩ ወይም ሕመሟ ቀላል እንደሆነ ተረዳሁ፡፡ ግን ምን እንዳመማት በትክክል አልተረዳሁም፡፡ “ሞዴስ” የሚለውን ቃል ስሰማ ለመጀመሪያ ጊዜ ነበር፡፡ አሁን ግን የሴት እቃ ከመሆኑ ሌላ ያሽልሻል ማለት ነው?” አልኳት፡፡ (በካህሳይ አብርሃ ብስራት ተፅፎ ባለፈው ቅዳሜ ከተመረቀው “የአሲምባ ፍቅር” መፅሃፍ የተቀነጨበ)

Published in ህብረተሰብ

“የሀገራችን ታሪክ የሚያተኩረው፣ የኢትዮጵያን ሕዝብ ደካማ ጐኖች በመተወን፣ ሥልጣን ላይ የሚወጡትንና ሥልጣናቸውን የሚያደላድሉትን በማሳቅ በማሞገስ ወይም በማንቋሸሽና በመርገም ላይ ነው፡፡ ይላል ተርጓሚው ዑስማን ሐሰን፡፡ ከዚህም የተነሣ ታሪክን በተመለከተ የተለያዩ አስተሳሰቦች በኢትዮጵያውያን ላይ ሊፈጠሩ ችለዋል፡፡ ታሪክን አሽቀንጥሮ መጣል፣ በታሪክ ውስጥ አልፈው የመጡትን ትውፊቶችን ጭምር መጣል ወይም መሳት ወይም ያለመፈለግ አዝማሚያ…በአንድ በኩል፤ በሌላ በኩል ደግሞ በተለያየ አረዳድ እና በተለያየ እውቀት (መረጃ) ይዞ መኖር፤ ከነዚህም ሌሎች ዓይነቶች የሚሆኑ ሞልተው በሚገኙበት ዓለም ውስጥ የወደቅን ሕዝብ የመሆናችንን ሐቅ ልብ አንለው ይሆናል እንጂ የማይታይስ አይደለም፡፡ እንዲህ ያለውን ሁኔታ የተመለከተው የሥነ ማኀበረሰብ መምሕር ዑስማን ሐሰን (ኤም ኤ) ከልብ የታሰበበትን የታዋቂውን ዊልፍሬድ ቴሲጀር የጉዞ ማስታወሻዎች ወደ አማርኛ መልሶ ሰሞኑን አውጥቷል፡፡

“ሀገረ ሀበሻና የሰገሌው አብዮት” ተብለው በአሥራ አንድ ምዕራፎች የቀረቡት የዊልፍሬድ ቴሲጀር ሥራዎች በአማርኛ መቅረባቸው ብቻውን አንድ ትልቅ ነገር ሲሆን፤ ተርጓሚው የጨመራቸው “መግቢያ” እና “ማጠቃለያ” የተባሉት ደግሞ ራሳቸውን የቻሉ ቁብ ያላቸው ሥራዎች ናቸው፡፡ ሃያኛው መቶ በኢትዮጵያውያን አንድ ተብሎ መቆጠር በጀመረበት ዘመን ላይ የቴሲጀር አባት የእንግሊዝ ሌጋሲዮን አዲስ “እንደራሴ” ሆነው ስለተሾሙ፣ ከጥቂት ወራት በፊት ካገቧት ባለቤታቸው ጋር በምሥራቅ በኩል ወደ ኢትዮጵያ ገቡ፡፡ ከድሬዳዋ ወደ ሐረር በማምራት ሃሮማያ ላይ ከነጓዛቸው እንዲያርፉ ያደረጓቸው የወቅቱ የሐረርጌ ገዥ ባልቻ አባ ነፍሶ በክብር ተቀብለው በአጀብ ወደ አዲስ አበባ ላኳቸው፡፡ በከብት ወር ፈጅተው አዲስ አበባ ገቡ ያን ጊዜ በሌጋሲዮኑ ግቢ (የዛሬው እንግሊዝ ኤምባሲ ግቢ) ውስጥ መደዳ ተሰልፈው የሚታዩ ሰፋፊ ጐጆ ቤቶች ብቻ ነበሩበት፡፡ ከነዚያ “ክብር ና የሣር ክዳን” ከነበራቸው ጐጆዎች በአንዱ የአምባሳደሩ የመጀመሪያ ልጅ የሆነው፣ ተጓዡና አዳኙ እንዲሁም የመጽሐፉ ፀሐፊ የሆነው ዊልፍሬድ ቴሲገር ተወለደ።

“በሀበሻ ሀገር የተወለድሁ የመጀመሪያው አውሮፓዊ” መሆኑን ሳይቀር ለይቶ ማየት የቻለው ቴሲገር ጀብድን ወዳድ ሆኖ ያደገ ነበር፡፡ ጭካኔን፣ ሁከትን፣ የተተረማመስን ነገር የመውደዱን ምክንያት በኢትዮጵያ ውስጥ በልጅነቱ የተመለከታቸውን የሰገሌ ዘመቻን፣ ከሰገሌ መልስ በጃንሜዳ ከአባቱ ጋር ተገኝቶ ያየው የግዳይ መጣል ሥርዓት የመሳሰሉትን ምክንያት ያድርገው እንጂ አባትየው ገና በልጅነቱ ጀምሮ ወደ ጫካ እየሰወዱት በወፎችና በሌሎች እንስሳት ላይ አነጣጥሮ እንዲተኩስ እያደረጉና በትላልቅ አውሬ አደናቸው ሁሉ እያስከተሉ ያሳደጉት ከመሆኑ ጭምር የመጣበት ነበር፡፡ በቤተሰቡ ታሪክና ታላቅነት ኩራትና ይሰማቸው የነበሩት አባቱ፤ ከአያት ቅድመ አያታቸው ጀምሮ እየተረኩላቸው ያደጉም ነበሩ፡፡ ቅድመ አያቱ የእንግሊዝ ፓርላማ ቻንስለር ነበሩ፣ አያቱ በታወቁት የዓለም ዐውደ ግንባሮች የተካፈሉ ጄኔራል ሲሆኑ በክሬምያ እና በመቅደላው ላይ ተካፍለዋል፡፡ አፄ ቴዎድሮስን ለመውጋት በመጣው የእንግሊዝ ጦር ውስጥ ከናፒዩር ቀጥለው አዛዥ ነበሩ፡፡ እነዚህን ሁሉ በምዕራፍ አንድ ያስተዋውቃል፡፡

በምዕራፍ ሁለት፤ ቴሲገር የኢትዮጵያን አጠቃላይ ታሪክ ሊዳስስ ሞክሯል፡፡ ማንኛውም አንባቢ የሚጠብቃቸው ከተለመዱትና ከታወቁት የኢትዮጵያ “ሂስትሪ” መሠረቶች ሌላ ምንም መጠበቅ የለበትም፡፡ ይህ “ሂስትሪ” ከሚያውቃቸው ሰዎች መካከል ዑለንዶርፍ የቴሲገርን መጽሐፍ ከመታተሙ በፊት የተመለከተውና የአርትዖት ሥራም የሠራበት መሆኑን አስቀድሞ በመግቢያው ስለገለጸ ብዙም የተለየ ነገር አንጠብቅም፡፡ በትምሕርት ቤቱ፣ በየዩኒቨርሲቲው፣ በየመጽሐፉ፣ በቱሪስት መምሪያውና በኛ ባለሥልጣኖች እንዲሁም የቋንቋ፣ የጐሣና የጐጥ ፖለቲካ ሊቃናት ጭንቅላት ውስጥ ተመስገው የኖሩ የታሪክ እውቀቶች፣ ሐሳቦችና ግንዛቤዎች ናቸው የቀረቡት፡፡ “ከመካከለኛው ምሥራቅ ወደ ሀገረ ሀበሻ ቀይ ባሕርን ተሻግረው (የገቡ ሰዎች) ሥልጣኔን ወደ ኢትዮጵያ አስገቡ፤ ክርስትና በፍሬምናጦስ በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ገባ፤ ፍሬምናጦስ ቀድሞ ጣዖትን አምላኪ የነበረውን “ኢዛናን ክርስትና አነሳው” “ለብዙ መቶ አመታት በአክሱሞች ቁጥጥር አስተዳደር ውስጥ ሳይገቡ የኖሩት የአገው ሕዝቦች ለአመጽ (ተነሳስተው) የአክሱምን ንጉሣዊ አስተዳደር (ወጉት)፡፡ (ገጽ 39) “እነዚህ የደቡብ አገዎች ክርስትናን የተቀበሉት ከዮዲት ዘመነ መንግሥት በኋላ ነበር፤ የዛጉዌ ሥርወመንግሥትን (?) መመሥረት የቻሉት ክርስትናን ከተቀበሉበት ዘመን (ከዮዲት ዘ.መ) ወዲህ ነው ወዘተ እያለ ይቀጥላል “ሰሎሞናዊ፣ “ዛጉዌዋዊ” የተባሉ “ሥርወመንግስታት” (ራሱን “ሥርወመንግስት የሚለውም”) ዓይነት የታሪካችን ስሞችንና ቃሎች መቸም እንኳን በቴሲገር ጽሑፍ በሮማ ልዑካን የተሠራውን ታሪክ ጠብተው ባደጉ የታሪክ ምሑራኖቻችንም ቢሆን ያልታየ ጉዳይ ነው፡፡

ራሱ ቴሲጀር የጨመራቸው የሚመስሉ አዳዲስ እይታዎችና ጥቆማዎችም እናገኛለን፡፡ “አፄ ምኒልክ በእንጦጦ እስከነገሱበት አመት ድረስ ሁሉም (ነገሥታት) የሚቀቡባት ሥፍራ አክሱም ነበረች፤” ይላል፡፡ ብዙም ሩቅ ሳይጓዝ የገዛ አያቱ የጄኔራል ናፒየር ጦር ምክትል የጦር አዛዥ ሆነው የዘመቱበትን የቴዎድሮስ ሥርዓተ መንግሥት የት እንደተፈፀመለትና የተቀባው የት እንደነበር ቢያውቅ እንዲያ ባልጻፈ ነበር፡፡ ሌሎች የታሪክ መጽሐፎችም አፄ ሰርፀድንግልንና አፄ ዘርዓ ያዕቆብን በንግሥ ሥርዓት ጉዳይ ወደ አክሱም መሄዳቸውን የተለየ አድርገው የሚጠቅሱላቸው ሁሎችም በአክሱም ባለመቀባታቸው ነበር፡፡ ፍሬምናጦስ በሮም ግዛተ አፄ የኢትዮጵያ እንደራሴ ሆኖ እንደነበርም ቴሲገር ጽፏል፡፡ ከየት እንዳገኘው ለማወቅ ይቸግራል፡፡ እሱማ ሩፊኖስን ይጠራል፡፡ ሩፊኖስ ግን በጭራሽ እንዲህ ያለ ጥቆማ አልጻፈም፡፡ ሩፊኖስ የፍሬምናጦስ ወንድም የነገረውን ሃቅ እንዳለ ቢጽፍም በብዙ ፀሐፊዎች የቀረቡ፤ “የተበረዘ፣ የተከለሰ” ከሚባለውም በላይ የሆኑ ልዩ ልዩ ሥራዎችን ማግኘት ይቻላል፡፡ ከነዚያ ዓይነቱም ቢሆን ግን እንዲህ ያለው ነገር አይገኝም፡፡ ደግሞም ፍሬምናጦስ ለጉብኝት ሔዶ ሳለ፣ በዚያው አትናቴዎስን አግኝቶት፣ ጳጳስነትን ሾሞት ወደ ኢትዮጵያ እንደላከውም ያስነብባል። አፄ ሱስንዮስ፣ “ያልሰማህ ስማ፣ የሰማህ አሰማ ይህንን እምነት የሰጠናችሁ መልካሙን አስበን ነበር፡፡ ነገር ግን ብዙ ሰዎች ተገደሉ፡፡

ለምሣሌ ጁሊየስ፣ ገብርኤል፣ ተክለጊዮርጊስ፣ ሠርፀ ክርስቶስ እና አሁን ደግሞ እነዚህ ገበሬዎች። ለነዚህ ምክንያቶች ስንል የአባቶቻችሁን እምነት መልሰንላችኋል ደስ ይበላችሁ” ብለው አዋጅ ካስነገሩ ከጥቂት ቀናት በኋላ ተገደሉ” ይላል፡፡ አፄ ሱስንዮስ በግድያ ነበር የሞቱት? አዲስ ነገር ይሆናል፡፡ አወጁት ተብሎ የተገለፀውም አዲስ ነገር ይሆናል፡፡ የቀረበው ቃል ያልተጻፈ አይደለም አይባልም፡፡ ለብዙዎች አዲስ ነገር ሊሆን ቢችልም ምናልባት የመገደሉም ነገር ይህን ዓዋጅ ለመጻፍና ለማስጻፍ በቻሉት በኩል የሚተረክ ይሆናል፡፡ የዜሲገርን መጽሐፍ በልዩ ጥንቃቄ ማንበብ የሚገባበት ምክንያት እንዲህ አንድ ሁለቱን መጠቃቀስ በጀመርንለት የምዕራፍ 2 “የሀገረ ሀበሻ ታሪክ” ብሎ ባቀረበው ላይ ብቻ አይሆንም፡፡ ማራኪ እና ብዙ መረጃዎችንና ዕውቀቶችን በምናገኝባቸው በተቀሩት ምዕራፎችም ውስጥ አልፎ አልፎ የተሰገሰጉ አይጠፉም፡፡ ባየውና በተመለከተው ነገር እየተነሳ የሚጨምራቸው አንዳንድ መበጠር የሚገባቸው ጉዳዮች አሉት፡፡ የቴሲገርም ሆነ የሌሎች ሥራዎች እንዲህ የመቅረባቸው አንድ ፋይዳም እነዚህንም እሚገልጡ መሆናቸው ነው፡፡

ቴሲገርን የሚወድዱትና የሚፈልጉበት ምክንያቶች ግን የጉዞና የጉብኝት ማስታወሻዎቹ ናቸው፡፡ ተራ ነገሮችን ቁምነገር አድርጐ ስለሚያቀርብ ለማንበብም ይማርካሉ፡፡ ትናንሽ መሰለው ሊታዩ የሚችሉ ነገር ግን ጥሩ የታሪክ ምሥክርነት ያላቸው መረጃዎችና እውቀቶችም ይገኝባቸዋል፡፡ ምንሊክ “ድሀው ሕዝቤ” እያሉ በሕመም አልጋ ላይ በዋሉበት ጊዜ ያለቅሱ እንደነበር፣ በኬንያ ሰሜናዊ ግዛት የቀሩ ሁለት የኦሮሞ ጐሣዎችን “ሕዝቤ” ብለውና በስማቸው እየጠሩ በመነጠላቸው ሲንገበገቡ መኖራቸውን የመሰለውን ታሪክ ከየት ልናገኝ እንችል ነበር? በሰገሌ ጦርነት ጊዜ ራስ ተፈሪ የሁለት ዓመት ተመንፈቅ የነበረውን ልጃቸውን (በኋላ ልዑል አልጋ ወራሽ አስፋወሰን) በቀይ አንቀልባ አሳዝለው፣ ዣንጥላ አስጠልተው ይዘው ወደ እንግሊዝ አምባሳደር (ወደ ጸሓፊው አባት) ወስደው በአደራ እንዲቀመጥላቸው ማድረጋቸው የመሰለውንም እናገኛለን፡፡ “ብዙ አውሮፓውያን የሀበሻን ቄሶች ያልተማሩ፣ አጉል እምነት አምላኪዎችና በዓለማዊ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩ መሆናቸውን ሲናገሩ ሰምቼ ነበር፡፡ ላሊበላ፣ እምረ ሀና (ይምርሐነ ሊል ነው ይምርሐነ ክርስቶስ፡፡) በነበርኩበት ጊዜ ግን ይህንን አባባል እውነት ሆኖ አላገኘሁትም፡፡

ቄሶቹ በሥርዓታቸው፣ በደግነታቸውና በአዛኝነታቸው የሀበሻ ትልልቅ ሰዎች መገለጫዎች ሆነው ነው ያገኘኋቸው፡፡” ቴሲገር በስተደቡብ በኩል ባደረገው ጉዞ ከየትኛውም የአውሮፓና የአሜሪካ የመጡ ሚሲዮናውያን በእንግድነት እያረፈባቸው ቢያልፍም፣ “ለእኔ በጣም ደግና እንግዳ ተቀባይ ቢሆኑም በነዚያ ቦታዎች መገኘቴ ግን አበሳጭቶኝ ነበር” ይላል፡፡ (ገጽ 61) በላሊበላ እርሱ ጉብኝት ሲያደርግ ከወልድያ በበቅሎ በሁለት ቀን ውስጥ በድምሩ የ15 ሰዓታት ጉዞ በማድረግ ገብቶ፣ ከአዲስ አበባ በአውሮፕላን እዚያ ድረስ ጐብኝዎችን እየወሰዱ ሊያስጐበኟቸው መታቀዱን ሰምቻለሁ ብሎ በዚያ ያዘነ መሆኑን ገልጿል (ገጽ 158) በ1948 በደቡብ ያደረገው ጉዞ ጫማውን እስኪቀደድ ድረስ አብቅቶት በጨንቻ፣ ኮንስና ተልተሌ አድርጐ ሜጋ ላይ ያለ የእንግሊዝ ቆንሲል ወደ ሞያሌው ወስዶት፣ በዚያው የነበረው የእንግሊዞች ወኪል ጆርጅ ዌብ ነበር ጫማው እንዲጠገንና አንድ ሰንደል ጫማ እንዲሰራለት ያደረገው፡፡ ከዚያ በኋላ ወደ ሰሜን አቅጣጫ የሶማሌዎችንና የጉጂዎችን ሀገር ጐብኝቶ በሀገረማርያም አድርጐ ዲላ በመድረስ፣ በአውቶቡስ ሻሸመኔ፣ ከዚያም አዲስ አበባ ገብቷል፡፡ የሞያሌው ጆርጅ ዌብ ጫማው ተቀድዶ ለመጀመሪያ ቀን ያየው እለት የነገረውን አስፍሯል፡፡ “ትናንት ሳይህ ልቤ [ክው ነበር] ያለው፡፡ ድሃ የሆነ እንግሊዛዊ ቼክ ሊለምነኝ የመጣ ነበር የመሰለኝ፡፡” ከዚህ ጉዞው ተመልሶ አዲስ አበባ ከደረሰ በኋላ ካርቱም ነበር የሄደው፡፡ በዚህ ዘመን ነበር ሱዳን ነፃ የወጣችው፡፡

ስለ ሱዳናውያንም ሲጽፍ፣ “ምናልባትም ከአፍሪካውያን ሁሉ በጣም የሚወደዱና ደግ የሆኑ ሰዎች” ብሎ ያደንቃቸዋል” ከሦስት ዓመት በኋላም እንደገና ለጉብኝት ተመልሶ ወደ ኢትዮጵያ ገብቷል፡፡ አሁን ደግሞ የአባይን ሸለቆ በመከተል ጣና ፣ ጐንደር፣ ሰሜን ተራሮች ከዚያ ላሊበላን በድጋሚ ተመልክቷል። መቅደላን፣ ከዚያ ወደ ሸዋ ገብቶ አንኮበርንና በልጅነቱ ጀምሮ ተቀርጾበት የቀረው ጦርነት የተካሄደበትን ሰገሌን ጐብኝቶ አዲስ አበባ ገብቷል፡፡ የሰገሌው “ግርግር” ተብሎ የሚጠራው፣ ከአዲስ አበባ 96 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በሚገኝ ዓውደ ግንባር ላይ ከወሎው ንጉሥ ሚካኤል ጋር የተደረገውን ጦርነት ከአንደኛው የዓለም ጦርነት ጋር ምን ያህል ይገናኛል? “ምን ያህል” ቀርቶ ምን ዓይነት ግንኙነት እንደሚኖረውስ ማን ይገምታል? እርግጥ ነው በሀገር ውስጥ ካሉ ጀርመናውያንና ቱርካውያን ጋር ልጅ ኢያሱ ያደርጉት የነበረውን ግንኙነት ጠቆም በማድረግ የኢያሱ ወገኖች የሚያይሉበት ሊሆን እንደሚችል እና ሌሎች ስስ የሆኑ ዓለምአቀፋዊ መነካኪያዎችን ለማውጣትና ለመግለጽ የተቻለባቸው የታሪክ ጽሑፎች አናጣም ይሆናል። ነገር ግን በሰገሌው ጦርነት ለልጃቸው ለኢያሱ ሥልጣን ማጣት የተነሱት ንጉሥ ሚካኤል ቢያሸንፉ ከጀርመኖችና እና ከቱርኮች ጋር ለተፋጠጡት እንግሊዝና ፈረንሳይም እንደ አንድ ሽንፈት ይቆጠር እንደነበር ምንኛ ታስቦ ይሆን! ተርጓሚው መምሕር ዑስማን ሐሰን “የሰገሌው አብዮት” በማለት የትርጉም ሥራው ከፊል ርእስ ማድረጉ ጥያቄ ይፈጥርና ለምን እንዲያ እንዳለው ለማወቅ ያጓጓ ይሆናል፡፡ እኔም መጽሐፉን ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁ ጊዜ እንዲሁ አስቤ ነበር ለማየት የፈለግኹት፡፡

ከማንበብ በፊትም ሆነ እያነበብኩት፣ ካነበብሁትም በኋላ ለምን እንዲያ እንደተባለ ለማወቅ ራሱን ተርጓሚውን ማግኘት እንዳለብኝ አስቤ ነበር፡፡ በመግቢያው ላይ ራሱ ቴሲገር “አብዮት” ብሎ እንደጠራው የተገለፀውም ሆነ፣ ቴሲገር ምዕራፎች (ገጽ 53) ከርእሱ ጀምሮ “የሰገሌው አብዮት” ማለቱና በውስጡም፣ በዚያው ወቅት ከእንግሊዝ ለጋሲዮን ወደ ውጭ የሚወጡ ሪፖርቶችም ሆኑ ሌሎች ወረቀቶች ያን “ግርግር” ተብሎ በኛ ዘንድ እንዲጠራ የተደረገውን ጦርነት “አብዮት” ብሎት እንደነበር መረዳቱም ቢሆን ጥያቄውን አያጠፋውም - ከተርጓሚው ራስ ያወርደው እንደሆን እንጂ፡፡ ተርጓሚው የሶሺዮሎጂው ምሑርና መምሕር ዑስማን ሐሰንም ቢሆን “መጀመሪያ ላይ እንዳልተዋጠለት ይገልጻል፡፡ “በኋላ ላይ ግን ወድጄዋለሁ” አለኝ፡፡ ለዚህም ያስከትል የነበረውን ለውጥ በማጤን እንደነበርም ጨምሮ አስረድቶኛል። የተርጓሚው መግቢያና ማጠናቀቂያ በ214 ገጾች ክትት ተደርገው ደቀቅ ባሉ የፊደል መጠናት የቀረቡልን ጽሑፎች በሙሉ የታዋቂው ተጓዥና አዳኝ የዊልፍሬድ ቴሊገር ሥራዎች ብቻ አይደሉም፡፡ የመጽሐፉን ዓይነት ለየት እንዲል ብቻ ሳይሆን፣ ጠቀሜታውንም ጨመር የሚያደርገው የተርጓሚው የራሱ ሥራዎች መሠመራቸውም ላይ ነው፡፡

“መግቢያ” እና “ማጠቃለያ” ተብለው የቀረቡ ምሑራዊ እይታዎችና ሙያዊ የጥናት ወረቀቶች አከል የሆኑ ሁለት ምንባባትም 51 ገጾችን ይዘዋል፡፡ ምናልባት ለምን አስፈለጉ ማለቱ ይቀድምብን ይሆናል፡፡ በተለይ “መግቢያ (ከተርጓሚው)” ተብሎ 22 ገጾች ማቅረቡን በመጀመሪያ እኔ ብቻ ሳልሆን ቀድመው ማንበብ የቻሉ ሌሎችም ጠቁመውኛል። እኔም ልክ እንደ ልብ ወለድ መጽሐፍ ያን ዘልዬ በሁለት ገጾች ከቀረበችው የቴሲጀር መግቢያ ጀምሬ ነበር ማንበቤን የቀጠልኹት - በኋላ እመለስበታለሁ ብዬ፡፡ ያን መግቢያ ሳነብብ ግን ሶሺዮሎጂስቱ ዑስማን ከሥነ ማኅበረሰብ ምሑርነቱ አኳያም ታሪክን በእንደምን ያለ አቀራረብ መመልከት እንደሚገባን፣ የትርጉም ሥራውን ለመተርጐም ወይም ለማቅረብም የተነሳሳበትንና ቁም ነገር አድርጐ የተመለከተበትን ግንዛቤውን የሚገልጽልን፤ ራሱን የቻለ እጅግ ሰፊ እና ከበድ ያለ ጉዳይን ነው በዚህ “መግቢያ” ብሎ በጠራው ጽሑፍ ያቀረበው። እንዲያውም፣ ከበጉ ሥጋ ቆዳው በልጦ የሚገኝበት ይመስለንና ለምን ለብቻ አያቀርበውም ወደ ማለት ወሰድ ሊያደርገን የሚችል ይኾናል፣ ግን በጉን ያለ ቆዳው ወይም ያለ ሥጋው በግ ብለን አንይዘውም፡፡ በዚያ መግቢያው በሥነ ማኅበረሰባዊ ኅልዮት ግንዛቤና እውቀት የተተነተነ ታሪክን በተለይም እኛ ኢትዮጵያውያን የተባልን ዛሬ የዕለት ተዕለት ጉዳያችን ለመኾን ያበቃንን የሀገራችንን የቀድሞ ዘመን ታሪኮቻችንን እንደምን አድርገን እንደያዝነው እና እንዴት መያዝ እንደሚገባ በቅንነት ያለ ስስት ያለውን መስጠቱን እናያለን፡፡

ማኅበረ ፖለቲካዊ ጥሪቶችን” ለጋራ ጥቅማችንና እድገታችን ልናውል እንደሚገባ፤ ያንንም ወድደን ሳይሆን ያለ ምርጫ መቀበል ያለብን መኾኑን፤ ከዚያ ተነስተን ያንን እንደሚገባው ራሳችንን በማስገባት አዎንታዊ ጉዞ መቀጠል እንዳለብን ነው ያ ጥናት አከል ጽሑፍ ሲጨመቅ ጠብ የሚያደርግልን፡፡ ለአብነት እጠቅስለታለሁ፡- “… በእያንዳንዳችን አቅምና ቁጥጥር ስር የሚኖሩት ብቸኞቹ ነገሮች የአባቶቻችንን ውርስና ቅርሶች እምነት መቀበልና (መቀጠል) ብቻ ነው። ለሀገራዊ ማንነት መሠረታዊ መነሻዎች በአግባቡ ለመገንዘብ ሁለት ነገሮችን በአንድ ላይ ማከናወን ይኖርብናል፡- አንድ፣ ያለ ፈቃዳችን ማቀበል፤ ሁለት፣ የተቀበልነውን ፈቅደን መቀጠል፡፡ (ገጽ 13) አንዲቷን እንደ ምርቃት እንጨምር፡- “ማንኛውም የጋራ ማንነት እውን እንዲሆን ተመሳሳይና ወጥ የኾነ አስተሳሰብ (እንዲኹም) ትርጉም ያለው ምልክት (አርማ) ያስፈልገናል፡፡” (ገጽ 18) እንዲህ ያለ ቃለ ምዕዳን የመሣሰሉ አናቅጽ ብቻ አይደሉም “መግቢያ” ብሎ ተርጓሚው ባቀረበው የራሱ ሥራ ያቀረበው፡፡ እነዚህን ለማምጣት ያስቻሉ ነባራዊ ኹኔታዎችንና ሙያዊ ሀቲቶችን በማቅረብና በምሑራዊ ሥራዎች በማስደገፍ የሚገልጻቸውን በመጨመር እንጂ፡፡ “ማጠናቀቂያው” ላይ ጥያቄ አይኖርም።

ከዋናው ሥራ ቀጥሎ የቀረበ ነው፡፡ ብዙ ጊዜ የኢትዮጵያን ታሪክ ከውጭም ኾነ ከሀገር ውስጥ የታሪክ ምሑራንና ጸሐፊዎች በመቅዳት ወይም በመተርጐም ለማቅረብ ሲፈለግ ብዙ የሚያንገበግቡ ነገሮች ይገጥሙና እነዚያን እንዴት ነው ማድረግ የምንችለው? ጸሐፊው ያለውን ቀይረን፣ ለውጠን፣ አርመን ሌላ ጉዳይ ይኾናል፡፡ እንዳለ ማቅረቡም ሌላ ችግር ነው፡፡ እንዳለ አለማቅረቡም ቢሆን ይበልጥ አጉዳይ ይኾናል፡፡ ዑስማን ቴሲገርን ተርጉሞ ያላንዳች ጣልቃ ገብነት የራሱን በራሱ ገጾች ካቀረበለት በኋላ፣ በዚህ ታሪካዊ እና የጉዞ ማስታወሻው ውስጥ ያሉትን ሳንካዎች፣ አጉል የሆኑ አረዳዶችና የተሳሳቱ ጥቆማዎችን በመነቃቀስ በመጨረሻዎቹ ገጾቹ አቅርቧል፡፡ በዚያውም፣ አስቀድሞ በመግቢያው ወደ አለፉ ታሪካችን እንዴት ባለ አቀራረብ መጠጋት እንደሚቻል ያላንዳች ምርጫ የምንቀበላቸውን ተቀብለን እንዴት እንደምናጤንም በተግባር ለአብነት ያህል ማቅረብ የቻለባቸው ገጾችም ናቸው፡፡ ይህን የዑስማንን ሥራ አስቀድሞ ከምናውቃቸው ወደ አማርኛ ተመልሰው ከቀረቡልን ታሪክና ታሪክ ቀመስ ሥራዎች ለየት ያለ ቦታ የምንሰጠውና ቁብ ያለው አድርገን ለማሰብ የሚያስችለንም እነዚህ ሁለቱ የተርጓሚው ሥራዎች የተጨመሩበትም መሆኑ ላይ ነው፡፡

Published in ባህል

በቅርቡ በአዲስ አበባ ከተማ የተጀመረውን የቤቶች ልማት ፕሮግራም ምዝገባ አስመልክቶ አስተያየታቸውን የተጠየቁ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ፕሮግራሙ የሚሳካ አይመስለንም ይላሉ፡፡ በርካታ የቤት ተመዝጋቢዎችም መንግስት ቃል የገባው የቤቶች ግንባታ ይሣካ ይሆን የሚል ጥርጣሬ አላቸው፡፡ ይሄንን መነሻ በማድረግ የቤት ፕሮግራሙን በተመለከተ የተቃዋሚ አመራሮቹ አይሳካም የሚሉበትን ምክንያት በዝርዝር እንዲያስረዱን ጠይቀናቸው የሰጡንን ምላሽ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡


“እንደ ብሄራዊ ሎተሪ በእጣ ቤት ማደል የኢኮኖሚ ስራ ነው ብዬ አላምንም”
አቶ ሙሼ ሠሙ
የባንክ ባለሙያና የኢዴፓ ሊቀመንበር
መጀመሪያ ማንም ዜጋ ቤት ማግኘት ያለበት በጥረቱ ነው ብዬ ነው የማስበው እንጂ ልክ እንደብሄራዊ ሎተሪ በእጣ ቤት ማደል የኢኮኖሚ ስራ ነው ብዬ አላምንም፡፡ መጨረሻ ላይ ማጣፊያው ያጥራል፡፡ መጀመሪያውኑ የኮንዶሚኒየም ቤቶች ሲታደሉ መንግስት እያንዳንዱ ቤት ፈላጊ የተወሠነ ገንዘብ አጠራቅሞ ባጠራቀመው ገንዘብ ላይ ድጋፍ ተደርጐለት በረጅም ጊዜ ብድር ቤት የሚያገኝበት እድል ቢያመቻች ኖሮ ዛሬ የሚሠሩት ቤቶች አጣብቂኝ ውስጥ አይገቡም ነበር፡፡ መንግስት ከዚህ አኳያ ሊገጥመው የሚችለው ችግር የገንዘብ አቅም ጉዳይ ነው፡፡ ገንዘቡ ከአሁን በኋላ ተጠራቅሞ ነው እንግዲህ ሠዎች የቤት ባለቤት የሚሆኑት። በዚህ መሀል መገንባት አለበት፡፡ ቤቱን ለመገንባት ደግሞ ወደ ብድር መግባት አለበት፡፡ የኢትዮጵያ መንግስትን አቅም እናውቀዋለን - 1.2 ሚሊዮን ቤት ለመገንባት የሚያስችል አቅም ሊፈጥር የሚችል ገንዘብ የተለየ ፈንድ ካላገኘ በቀር ከየትም ሊያመጣ አይችልም፡፡ ገንዘብ ማተም ውስጥ ካልገባ በቀር ወይም ደግሞ በጣም ከፍተኛ ገንዘብ ከቻይናና ከህንድ የሚያገኝበትን ሁኔታ ካላመቻቸ በቀር እነዚህን ቤቶች በሰባት አመት ውስጥ ሊገነባ የሚያስችለውን አቅም ሊያገኝ አይችልም፡፡ ሁለተኛው ይሄንን ቤት ለመገንባት የሠው ሃይል ጥያቄ አለ፡፡ 1.2 ሚሊዮን ቤቶች ለመገንባት በቤት ግንባታ እውቀት ያላቸው በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሠዎች ያስፈልጋሉ፡፡ እነዚህ ሠዎች ከየት ነው የሚመጡት? ሶስተኛው ደግሞ የተፈጥሮ ሃብት ነው - መሬት፣ ድንጋይ፣ ብረት፣ ሲሚንቶ፣ ጠጠር የመሣሠሉት በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ ከየት ነው ሊመጡ የሚችሉት? እነዚህ መሠረታዊ ጉዳዮች በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ ይሟላሉ ብዬ አላምንም፡፡ የተባለው ፕሮግራምም ይሣካል ብዬ አልገምትም፡፡
“መንግስት የዜጐች ቤት ሠሪ ሊሆን አይችልም”
የተከበሩ አቶ ግርማ ሠይፉ
የፓርላማ አባል- የአንድነት ፓርቲ አመራር
እኔ በግሌ ትርጉም የሚሠጥ ነው ብዬ አስቤውም አላውቅም፡፡ የህዝቡን ስሜት ለመግዛት ምን ማድረግ እንዳለባቸው ሲያስቡ የመጣላቸው እና የታያቸው አንዱ መንገድ ነው፡፡ አሁን እየተደረገ ያለው ነገር በዋናነት የሃገር ውስጥ ቁጠባ አነስተኛ ነው ከሚለው በመነሣት የመጣ ነው፡፡ እርግጥ ነው የሃገር ውስጥ ቁጠባ አነስተኛ ነው ነገር ግን ህዝቡ ዝም ብሎ አይቆጥብም። ስለዚህ መንግስት ህዝቡ እንዲቆጥብ አንድ ነገር ራቅ አድርጐ ሠቅሎ ማሣየት ነበረበት፡፡ የቤቶች ፕሮግራሙ ዋና አላማው በሃገር ውስጥ ያለውን የቁጠባ ባህል ከፍ ማድረግ ነው፡፡
ስለዚህ ቤት በማግኘትና ባለማግኘት ቁም ነገር ላይ ተመስርቶ የተዘጋጀ ሣይሆን የሃገር ውስጥ ቁጠባን ለማሣደግ ተብሎ ነው፡፡ ከዚያ ውጪ ግን በመርህ ደረጃ መንግስት የዜጐች ቤት ሠሪ ሊሆን አይችልም፡፡ ለምሣሌ ባለፈው ክቡር ጠ/ሚኒስትሩ መቶ ሺህ ቤቶች ሠርተናል ብለው በኩራት ተናግረዋል፡፡ እነሱ ጉልበትና ስልጣን ስላላቸው የሠው ስራ ቀምተው በመስራታቸው ሊኩራሩ አይገባም፡፡ በ1998 ለተመዘገቡ 450 ሺህ ቤት ፈላጊዎች በስምንት አመት ጊዜ ውስጥ ቤቶች ሰርተን እናጠናቅቃለን ብለው ይኸው ስምንት አመት አልፎ እንኳ 100ሺህ ቤቶች መስራት አልቻሉም፡፡ ጅምሮቹን ጭምር ነው 100 ሺህ ቤቶች ሠርተናል ያሉት። ለእነዚህ ቤቶች አንድ ጊዜ መሠረት በመጣል፣ አንድ ጊዜ በማስመረቅ ሌላ ጊዜ ቁልፍ በመስጠት አምስት ጊዜ ይወራና 500ሺህ ያስመስሉታል። አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የተሠሩት ቤቶች 100ሺህ ናቸው - እስክስታው ዘፈኑ ግን ሚሊዮን ነው። በተቃራኒው ግን በማህበር በመሣሠሉት ከዚህ ከላይ ቤቶች ተሠርተዋል፡፡ ከዚህ አንፃር መታየት ያለበት ፕሮግራሙ አንደኛ አላማው ለዜጐች ቤት መስጠት ሣይሆን የቁጠባ ባህሉን ማበረታታት ነው፡፡ ግን በየአመቱ ትንሽ ትንሽ ነገር እየሠጡ በማሣየት ሠዎች በተስፋ እንዲቆጥቡ ይደረጋል፡፡ በዚህ ማሣያው ቁጠባውን ያቋረጠ ይሠረዛል ይላል፡፡ ቤቱን ይሠሩታል አይሠሩትም ለሚለው በእርግጠኝነት አይሠሩትም፡፡ የሆነ አስማት እንኳ ተፈጥሮ ቢሠሩት ትክክል ነው ብዬ አላምንም። ሌሎች በሪል ስቴት ውስጥ ተሣትፈው ይሄን ሊያደርጉ የሚችሉ ሠዎችን ስራ እየቀሙ ነው እንሰራለን የሚሉት፡፡ መንግስት ዜጐች በተመጣጣኝ ዋጋ ቤት ማግኘት አለባቸው የሚል አቋም ሊይዝ ይችላል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ ቤትን ውድ የሚያደርገው አንደኛው መሬት ነው - ራሱ ሲሠራ በነፃ መሬት ይወስዳል፡፡ የግንባታ ግብአትም ከቀረጥ ነፃ እንዲገባ ያደርጋል፡፡ ስለዚህ በርካሽ ዋጋ የመስራት አቅምን ለራሱ ያመቻቻል፡፡ ይህን አቅም ወደ ግል ሴክተሩ አዘዋውሮ እነዚህን ማበረታቻዎች ሠጥቶ ሜዳውን ለነሡ ቢለቅ ነበር የሚሻለው፡፡ አሁን ግን ፕሮግራሙን ወደ ገጠር አካባቢዎችም ለማስፋት እቅድ ያለው ይመስላል። በየቦታው የተከፈቱ የንግድ ባንክ ቅርንጫፎችም ለዚህ የተመቻቹ ናቸው፡፡ ሠው አሁን ቆጥቦ በኋላ ባይደርሠው ገንዘቡን መውሠድ እንደሚችልም አማራጭ ተቀምጧል፡፡ ነገር ግን ቆጣቢው ኋላ ላይ የሚያገኘው ገንዘብ በዋጋ ንረት የተጐዳና የመግዛት አቅም የሌለው ነው የሚሆነው፡፡

“መንግስት የሚመረጠው ነጋዴ እንዲሆን አይደለም”
አቶ ቡልቻ ደመቅሣ
የፋይናንስ ባለሙያና የመድረክ አመራር አባል
የቤቶች ፕሮግራሙ የተዘረጋው የፖለቲካ ጥቅም ለማግኘት ነው፡፡ የእነዚህ ፕሮግራም ተሣታፊዎች የኢህአዴግ አባል እንዲሆኑ ነው የሚደረጉት፡፡ ለምሣሌ አንድ ሠው ቤት ልስራ ብሎ 40/60 የሚባለው ውስጥ ቢገባ መጀመሪያ ማረጋገጥ የሚፈልጉት የኢህአዴግ አባል መሆኑን ነው፣ ስለዚህ ይሄ ጠቃሚ ሳይሆን ጐጂ ነው። መንግስት የሚመረጠው ነጋዴ እንዲሆን አይደለም። ፍርድ እንዲሠጥ፣ የፖሊስ ስራ እንዲሠራ፣ ጉምሩክ እቃ ሲገባ ቀረጥ እንዲያስከፍል፣ መሬት በደንብ እንዲለማ፣ የኢኮኖሚ ልማት እንዲመጣ ነው እንጂ ንግድ ውስጥ ገብቶ እንደ ተራ ነጋዴ ለመቸብቸብ አይደለም፡፡ ዞሮ ዞሮ ደግሞ ይሄ ሃገራችንን ይጐዳል፡፡ የአለም ንግድ ድርጅት አባል መሆን ያልቻልነው እኮ መንግስት ከንግድ ውስጥ መውጣት ባለመቻሉ ነው፡፡ በዚህ ድርጅት ውስጥ አለመግባት ደግሞ ለዘለቄታው ጉዳት አለው፡፡ ለኢህአዴግ ንግድ ፖለቲካ ነው። በንግዱ የፖለቲካ ትርፍ ማግኘት ይችላሉ፡፡ አሁን ለህዝቡ ቃል እንደገባው ተሣክቶለት ቤቱን ቢሠራም ትክክል አይደለም፡፡ ገንዘብ ከዚህ ሁሉ ሠው መሠብሠቡ በራሱ ቀላል አይደለም። የመንግስት ዋነኛ ስራው መሆን የለበትም፡፡ የመንግስት ሠራተኛ የሚቀጠረው የመንግስት ስራ ተብለው የተለዩትን ለመስራት ብቻ ነው፡፡ ግብር መሠብሠብ እንጂ ከህዝቡ ጋር እየተጋፉ ገንዘብ ለማስገባት አይደለም፡፡ አሁንም አጥብቄ የምናገረው ይህ የመንግስት ተግባር አለመሆኑን ነው፡፡ የመንግስት ሥራ ዳር ድንበር መጠበቅ፣ ፍትህ ማስፈን፣ መንገድ መገንባት እንጂ ብር እያበደሩ ቤት መስራት አይደለም፡፡

“የቤት ፕሮግራሙ ለቀጣዩ ምርጫ የታለመ ይመስላል”
ዶ/ር መረራ ጉዲና
የፖለቲካ ሣይንስ ምሁር እና የመድረክ አመራር አባል
መንግስት ብዙ ድስቶችን ጥዶ ነው የሚንቀሣቀሰው፡፡ አንደኛው ድስት ይሄ መሆኑ ነው፡፡ ዋናው ግን ይሄ የቤት ፕሮግራም ለ2007 ምርጫ የታለመ ይመስላል፡፡ የዚያን ጊዜ እኛን ካልመረጣችሁ ቤት አታገኙም ሊሉ ይመስላል ዳር ዳር የሚሉት፡፡ አሁን እንግዲህ ወደ 2 ሚሊዮን ቤት ነው እንሰራለን ያሉት፡፡ ይሄ ደግሞ በኛ አቅም አጠያያቂ ነው፡፡ ደግሞ ሁሉን አይነት ሠው ነው የሚመዘግቡት፡፡ ውጤቱን እንግዲህ ውሎ አድሮ ማየቱ ይሻላል፡፡ የኔ ጥርጣሬ ግን የ2007 ምርጫን ታሣቢ አድርገው ነው የሚል ነው፡፡ ጨዋታው ቀላል አይደለም፡፡
ቤት መስራት ብቻ ሣይሆን ከዚያ ጋር ብዙ የተያያዙ ነገሮች አሉ፡፡ መሠረተ ልማቱ መጨመር አለበት- ውሃ፣ መብራት፣ መንገድ፣ ስልክ አለ። እኒህን ሁሉ ማሳካት ከቻሉ ጥሩ ነው፣ ግን አይመስለኝም፡፡

(1. የእንግሊዝኛ ቋንቋ 2. ኮምፒዩተር 3. ኢንተርኔት … ናቸው ስጦታዎቹ። መፃህፍት እንደልብ ለማንበብና ስኬትን ለመቀዳጀት) እውቀት የዶ/ር ቤን ካርሰን ታሪክ ምስክር ነው። በህፃንነቱ “ደደብ ነኝ” ይል ነበር - ትምህርት ጨርሶ የማይገባው። ከድህነት ጋር በምትታገል እናቱ ግፊት መፅሃፍ ማንበብ ጀመረ። በአንጎል ቀዶ ህክምና በቀዳሚነት የሚጠቀስ ሃኪም ለመሆን በቃ። በ2016 ለአሜሪካ ፕሬዚዳንትነት ይወዳደራል ተብሎ ይጠበቃል። “ተአምር” መስራት የሚቻልበት ዘመን ላይ ደርሰናል። ከሃያ አመታት በፊት በፍፁም የማይሞከሩ ነገሮች፣ ዛሬ በቀላሉ በመዳፋችን ውስጥ ልናስገባቸው እንችላለን። እስቲ አስቡት። በዚህ ሳምንት ብቻ፣ ከሁለት ሺ በላይ በእንግሊዝኛ የተፃፉ አዳዲስ የልብወለድ ድርሰቶች በኢንተርኔት አግኝቼ ኮምፒዩተሬ ውስጥ አስቀምጫለሁ - በ2012 እና በ2013 የታተሙ ተወዳጅ (bestseller) መፃህፍት ናቸው። በመቶ እና በሺ የሚቆጠሩ አዳዲስ መፃህፍት ማግኘት ይቅርና፣ ሦስት አራት አዳዲስ መፃህፍት ማግኘት ምን ያህል ብርቅ እንደነበር አታስታውሱም? ለነገሩ፣ ለብዙ ሰዎች ዛሬም ድረስ ብርቅ ነው።

የልብወለድ ድርሰቶችን ለጊዜው እንርሳቸው። ከአንደኛ ክፍል ጀምሮ እስከ ሃይስኩል፣ የሂሳብም ሆነ የተፈጥሮ ሳይንስ መማሪያ መፃህፍት፣ ከዩኒቨርስቲ የ‘ፍሬሽማን’ ትምህርት እስከ ማስተርስ ዲግሪ ድረስ፣ ከኤሌክትሪክ ምህንድስና እስከ ሕክምና፣ ከቢዝነስ ማኔጅመንት እስከ አለማቀፍ ዲፕሎማሲ… በመላው አለም እጅግ የሚፈለግ ውድ መፅሃፍ በየአይነቱ “በገፍ” ቢቀርብልን ብላችሁ አስቡ። ባለፉት ምዕተ አመታት የተፃፉ ዘመን የማይሽራቸው የሳይንስ መፃህፍትን ከፈለጋችሁ… ሞልቷል። አዳዲስ የዘመናችን ምርጥ የሳይንስ፣ የቴክኖሎጂና የመማሪያ መፃህፍትም እንደልብ ነው። እድሜ ለኢንተርኔት! በሺ ከሚቆጠሩት የትምህርት መፃህፍት መካከል፣ ለሙከራ ያህል ሁለት መቶ የሚሆኑትን ሰሞኑን ኮምፒዩተሬ ላይ ጭኛቸዋለሁ። አንዳንዶቹን ገለጥ ገለጥ አድርጌ አይቻቸዋለሁ። ባለፈው አመት ወይም ባለፉት ስድስት ወራት የታተሙ አዳዲስ የትምህርት መፃህፍትን እንዲህ እንደልብ ማግኘት “ተአምር” አይደለም? በቢዝነስ ጉዳዮች ዙሪያ እንደ ፎርብስ እና ዘ ኢኮኖሚስት የመሳሰሉ መፅሄቶች ሞልተዋል። የቴክኖሎጂና የሳይንስ ዘገባዎችን ወይም የጥናት ውጤቶችን ለመከታተልም፣ እንደ ፖፑላር ሜካኒክስ፣ ኔቸር፣ ዋየርድ፣ ናሽናል ጂኦግራፊ የመሳሰሉ መፅሄቶች አሉ። አዳዲስ የሰሞኑ እትሞቻቸውን በኢንተርኔት ወደ ኮምፒዩተሬ ገልብጬ አየት አየት እያደረግኳቸው ነው።

ስልጡን የፖለቲካ ባህል በቀጥታ ለማየት የሚፈልግ ካለም ምንም አይቸገርም። የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ወይም ቃል አቀባያቸው ለጋዜጠኞች የሚሰጡትን መግለጫ በቀጥታ መከታተል ይችላል። በአሜሪካ፣ የኮንግረስና የሴኔት ምክር ቤት ውስጥ የሚካሄዱ ክርክሮችን፣ በዚያው ሴኮንድ በቀጥታ ሲሰራጩ መመልከትስ? ከአራቱ የሲ-ስፓን ቻናሎች መካከል እያማረጡ መመልከት ነው። የምክር ቤት አባላት፣ የአክብሮት ስነምግባርን ሳይጥሱ፣ የመንግስት ሚኒስትሮችንና ከፍተኛ ባለስልጣናትን ወጥረው ሲያፋጥጡ ይታያሉ። የሳይንስና የቴክኖሎጂ ሰዎች እድሜ ይስጣቸውና፣ እንደየዝንባሌያችን እያማረጥን ያሻንን ያህል ማንበብና መከታተል የምንችልበት ዘመን ላይ ደርሰናል። ሙሉ ትኩረታችንን የሚጠይቅ ትምህርታዊ መፅሃፍ ማንበብ፣… ምን ያህል እንደሚመስጥና እንደሚያስደስት ታውቁት ይሆናል። ግን በየመሃሉ አረፍ ብሎ መንፈስን ማደስ ያስፈልግ የለ? ለምሳሌ፣ ቀለል ያለ፣ ልብ አንጠልጣይ የልብወለድ ድርሰት ማንበብ፣ ጥሩ የመዝናኛ ዘዴ ነው። ምን ጠፍቶ! አምናና ዘንድሮ በአሜሪካ የታተሙ አዳዲስ የልብወለድ መፃህፍት ሰሞኑን “በገፍ” አግኝቻለሁ።

ግን፣ በ20ኛው ክፍለዘመን፣ በልብ አንጠልጣይ የልብወለድ ድርሰት ገንነው ከሚጠቀሱ ደራሲዎች መካከል አንዱ የሆነው ሚኪ ስፕሌን ትዝ አለኝ። የስፕሌን ድርሰት ባገኝ… ብዬ በኢንተርኔት ፈለግሁ። 13 ድርሰቶቹን አገኘሁና፣ በ5 ደቂቃ ውስጥ ሁሉንም ወደ ኮምፒዩተሬ ገለበጥኳቸው። አንዱን መርጬ አነበብኩታ። በእርግጥም ዘና አደረገኝ። በዚያው አጋጣሚ ግን፣ በቪዲዮ፣ በድምፅ እና በፅሁፍ የተዘጋጁ የእንግሊዝኛ ቋንቋ መማሪያዎችን አይቻለሁ - ብዛታቸውና አይነታቸው እንዲህ ቀላል አይደለም። ከነባሮቹና ከአዳዲሶቹ የቋንቋ መማሪያዎች መካከል እየመረጥኩ ወደ ኮምፒዩተሬ መገልበጥ ነው የሚቀረኝ። በመላው አለም በጣም የሚፈለጉ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ማስተማሪያ መፃህፍትን ብቻ ሳይሆን፣ በድምፅና በቪዲዮ የተዘጋጁ አጋዥ መማሪያዎችን እንደ ልብ ማግኘት! “ምናለ፣ ይሄ ሁሉ እድል፣ ከአስር አመት ከሃያ አመት በፊትም በኖረ” ብዬ መቆጨቴ አልቀረም። ግን፣ አሁን መገኘቱም “ተአምር” ነው። ይልቅ፣ ይህን እድል ለመጠቀም መትጋት ነው የሚሻለው። ቀለል ባለ ልብወለድ መፅሃፍ ዘና ካልኩ በኋላ ወዲያውኑ ለሥራዬ በቀጥታ የሚጠቅመኝን መፅሃፍ ላነብ አልኩና… እንደአጋጣሚ ሃሳቤን ቀየርኩ። አልነገርኳችሁም እንጂ፤… በዚህ ሳምንት፣ ከልብወለድ ድርሰቶች በተጨማሪ፣ አንድ ሺ የሚሆኑ አዳዲስ “የሕይወት ታሪክ” መፃህፍትንም በኢንተርኔት ወደ ኮምፒዩተሬ ገልብጫለሁ።

ታዋቂው ሥራ ፈጣሪና ቢሊዮነር ሪቻርድ ብሮንሰን በ2011 ያሳተመው የግል የህይወት ታሪክ፣ የአሜሪካዊቷ ፖለቲከኛ ሳራ ፓይሊን፣ የበርማዊቷ የፖለቲካ መሪ አንሷን ሱኪ የህይወት ታሪኮች … በኢራቅ ጦርነት ብዙ አሸባሪዎችን በመግደል ሪከርድ የሰበረው ክሪስ ካይል ያሳተመው መፅሃፍ ሳይቀር… ብቻ ምን አለፋችሁ? በያዝነው የሰኔ ወር “ቤስትሴለር” ሰንጠረዥ ውስጥ ቁንጮውን ቦታ የተቆጣጠሩ መፃህፍት ሁሉ ቁጭ ብለው ለመነበብ ይጠብቃሉ። አንድ በአንድ አየኋቸው… የቀድሞው የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ቶኒ ብሌር ያዘጋጁት መፅሐፍ፣ የጆርጅ ቡሽ መፅሃፍ… እነዚህ ቆየት ያሉ ናቸው። ሌላ ጊዜ አነባቸዋለሁ። አዳዲሶቹንም አየሁ - ታዋቂው የአንጎል ቀዶ ህክምና ባለሙያ ዶ/ር ቤን ካርሰን ያሳተሙት መፅሃፍ ላይ ደረስኩ። በቅርቡ ከፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ጋር በትልቅ አመታዊ ጉባኤ ላይ ንግግር እንዲያቀርቡ ተጋብዘው የነበሩት ጥቁሩ አሜሪካዊ ቤን ካርሰን፣ ኦባማን በመተቸት ባቀረቡት የግማሽ ሰዓት ንግግር “አጃኢብ” ሲባልላቸው እንደሰነበቱ አውቃለሁ። ከኦባማ ጋር የሚያለያያቸውን ሃሳብ ዶ/ር ካርሰን ሲገልፁ፣ ድሆችን እንደግፋቸው በሚል ሰበብ የአገሪቱ ዜጎች የመንግስት ጥገኛ እንዲሆኑ እየተደረገ ነው በማለት ተናግረዋል።

አሜሪካ የተመሰረተችው ግን፣ ዜጎች ምንም ድሃ ቢሆኑ እንደየጥረታቸው ራሳቸውን ችለው የሚበለፅጉባት የነፃነት አገር እንድትሆን ነው ይላሉ - ዶ/ር ካርሰን። ይህን ሃሳባቸው ለማስረዳትም ነው አዲስ መፅሐፍ ያሳተሙት። ሃብታሞችንና ድሆችን የሚለያቸው ምንድነው? ዶ/ር ካርሰን ስለ ድህነትም ሆነ ስለ ሃብታምነት ቢናገሩ ያምርባቸዋል። ያለፉበት ሕይወት ነው። ከችጋር ወደ ብልፅግና እንዴት እንደተሸጋገሩ መነሻና መድረሻውን ያውቁታል። መፅሃፋቸውን አግኝቼ ላነበው ከተዘጋጀሁ በኋላ ነው፣ ካሁን በፊት ያሳተሟቸውን የመፃህፍት ዝርዝር ያየሁት። የመጀመሪያው መፅሃፍ “ጊፍትድ ሃንድስ” በሚል ርዕስ የታተመ ነው። ርዕሱን አስታወስኩት። መፅሃፉን ባላነበውም፣ ፊልሙን አይቼዋለሁ። ለካ፣ ኩባ ጉዲን የተወነበት ያ ምርጥ ፊልም፣ በዶ/ር ቤን ካርሰን የህይወት ታሪክ ላይ የተመሰረተ ነው። ከልጅነት እስከ እውቀት፣ የሕይወት ታሪካቸውን ባሰፈሩበት መፅሃፍ ውስጥም፣ ወደ ኋላ መለስ ብለው በድህነትና በ“ደደብነት” ያሳለፉትን የልጅነት ጊዜ ይተርካሉ። ስኬታማ ሰው ለምልክት ያህል በማይታይበት የድሆች ሰፈር ውስጥ ነው፣ ሕፃኑ ቤን ካርሰን ያለ አባት ያደገው። “እንደ እገሌ ስኬታማ እሆናለሁ” የሚያስብልና በአርአያነት የሚጠቀስ ሰው አልነበረውም - በቤተሰቡም ሆነ በሰፈሩ ውስጥ። ያልተማረችና ማንበብ የማትችል የካርሰን እናት፣ ሁለት ልጆቿን ለማሳደግ ያላየችው መከራ የለም። የሃብታሞችን ሰፈር ስታካልል ነው የምትውለው።

የሃብታሞችን ቤት በማፅዳት በምታገኛት አነስተኛ ገቢ ካርሰንና ወንድሙ ፆም እንዳያድሩ ብቻ ሳይሆን፣ ከትምህርት እንዳይርቁም ከንጋት እስከ ምሽት ትሰራለች። የእለት ተእለት ልፋቷ ትዕግስትን የሚፈታተን ቢሆንም፣ እጅግ የሚከነክናትና የሚያንገበግባት ግን፣ የድካሟን ያህል ውጤት አለማየቷ ነው። ልጆቿ፣ በየእለቱ ወደ ትምህርት ቤት መሄዳቸው ባይቀርም፣ ጠብ የሚል እውቀት አልቀሰሙም። ካርሰን እንደ ወንድሙ ክፍል ውስጥ “ሲማር” ይውላል፤ አስተማሪ አንዳች ጥያቄ ሲሰነዝር፣ ሌሎቹ ተማሪዎች መልስ ለመስጠት ይሻማሉ - እውቀታቸውን ለማሳየት። ግን፣ ካርሰን ሲጠየቅ ማየትም ያጓጓቸዋል - መመለስ ሲያቅተው ወይም ከጥያቄው ጋር የማይገናኝ ነገር ሲዘባርቅ መሳቅ ለምደዋል። ፈተና ሲመጣ፣ ካርሰን ከሌሎቹ ተማሪዎች ጋር አብሮ ይፈተናል። ተማሪዎች የፈተና ውጤታቸውን በኩራት ይናገራሉ፤ 25 ከ25 የሚደፍን ይኖራል፣ አነሰ ቢባል 20 የሚያመጣም ይኖራል። ካርሰን ድምፁን ዝቅ አድርጎ የራሱን ውጤት ይናገራል። አስተማሪዋ በደንብ አልሰማቸውም… “Nine?” በጣም ጥሩ ነው፤ 9 ከ 25? በጣም ተሻሽለሃልሳ! አለችው... ደስ ብሏታል። ካርሰን አስተማሪዋን ሊያርማት ይሞክራል - “Nine” ሳይሆን፣ “None” በማለት። ከፈተናው ጥያቄዎች ውስጥ አንዱንም በትክክል አልመለሰም፤ ዜሮ ነው ያመጣው። እንደተለመደው ተማሪዎቹ ይስቁበታል። ሲስቁበት አይከፋውም።

ራሱም ቢሆን፣ “ትምህርት አይገባኝም፣ ደደብ ነኝ” ብሎ በግልፅ ይናገራል። እናቱ ግን በዝምታ አታልፈውም። “ደደብ አይደለህም፤ አንጎል አለህ አይደለም?” ትለዋለች። “አዎ” ይላል እያመነታ። “ስለዚህ፤ አንጎልህን ተጠቀምበት። አለም ሁሉ በእጅህ ናት” ትለዋለች። ባትማርም፣ በጣም አስተዋይና ብልህ እናት ናት። የካርሰን እናት፣ ልጆቿ ስኬታማ መሆን እንደሚችሉ ከምር ታምናለች። እንዴት ስኬታማ እንደሚሆኑ ነው ያላወቀችው። ማሰብ ማሰላሰሏን ግን አላቋረጠችም። የሰፈሯን የድህነት አኗኗር በደንብ ታውቀዋለች። የሃብታሞች ሰፈር ሄዳ ቤት ስታፀዳም አኗኗራቸውን ትመለከታለች። ድሆቹንና ሃብታሞቹን የሚያለያቸው ምንድነው? አስተዋይ መሆኗ ጠቀማት። አንድ ቀን፣ በሃብታም ቤተሰብ መኖሪያ ቤት ውስጥ ሰፊውን ክፍል እያፀዳችና ቴሌቪዥን የተቀመጠበትን አካባቢ እየጠራረገች ሳለ… ተገለጠላት። ተደራርበው የተቀመጡት መፃህፍት ቴሌቪዥኑን በከፊል ከልለውታል። አንዳንዶቹ መፃህፍት ገለጥ ገለጥ ተደርገው ተቀምጠዋል። ቀና ስትል… ያን የሚያክል ሰፊ ክፍል፣ ከወለል እስከ ጣራ ድረስ… መደርደሪያው ሁሉ በመፃህፍት ተጠቅጥቋል። በቃ! ገባት። ያን እለት በየቦታው ለሥራ ስትደክም ውላ ማታ ወደ ቤት ስትመለስ፣ ካርሰንና ወንድሙ አሮጌ ቴሌቪዥን ላይ አፍጥጠው አገኘቻቸው። ቴሌቪዥኑን አጠፋችው። “ከዛሬ ጀምሮ፣ ቴሌቪዥን የምታዩት በሳምንት ሁለት ቀን ብቻ ነው” አለቻቸው።

ለምሳሌ፤ የተማሪዎች የጥያቄና መልስ ውድድር ማየት ይችላሉ። “ሁለት ቀን ብቻ? ሌላውንስ ጊዜ ምን እንሰራበታለን?” ብለው ጠየቁ። “ይህንን ጥያቄ ነበር ከናንተ የምጠብቀው። ምን እንደምታደርጉ እነግራችኋለሁ። ቤተመፃህፍት ትሄዳላችሁ። በሳምንት ሁለት መፅሃፍ ታነባላችሁ” ስትላቸው፣ የምሯን አልመሰላቸውም። መፅሃፍ ማንበብ የሚባል ነገር በእውናቸውም በህልማቸውም መጥቶላቸው አያውቅም። እንግዲህ ምን ይደረጋል? ከቤተመፃህፍት በውሰት መፅሃፍ ማምጣት የግድ ቢሆንም፣ የውሸት “አንብቤዋለሁ” ብሎ መመለስ እንደሚቻል ማሰባቸው አልቀረም። ሃሳባቸውን ያወቀች ይመስል፣ ሌላ ትዕዛዝ ጨመረችላቸው። “ያነበባችሁትን ቁምነገር፣ በየራሳችሁ አገላለፅ አሳጥራችሁ ትፅፉና ለኔ ትሰጡኛላችሁ” አለቻቸው። መፅሃፍ ማንበብ፣ ለካርሰንና ለወንድሙ ቀላል አልሆነላቸውም። ትግል ነው። ግን ደግሞ፣ መፃህፍቱ ውስጥ በሚያገኟቸው አስደናቂ ታሪኮችና እውቀቶች… ተገርመዋል። እስካሁን የማያውቁትና ጨርሶ ያልጠበቁት አይነት ልዩ ደስታ አግኝተውበታል። ብዙም ሳይቆይ፣ መፅሃፍ ማንበብ፣ “ግዴታ” መሆኑ ቀረ።

በንባብ ፍቅር፣ መፅሃፍ እንደያዙ ሌሊቱ ይጋመሳል። መፅሃፍ አንብቡ እያለች ስትወተውታቸው የነበረችው እናት፣ ቶሎ አንብበው በጊዜ እንዲተኙ መምከር ጀመረች። ካርሰን፣ “ደደብ” እንዳልሆነ ገባው። የሳይንስም ሆነ የሂሳብ፣ የቋንቋም ሆነ የታሪክ ትምህርቶችን ሁሉ በቀላሉ መረዳት እንደሚችል ሲያይ፣ ለማመን ከብዶት ነበር። ግን፣ የፈተና ውጤቱም በአጭር ጊዜ ውስጥ ተሻሽሏል። በሁለተኛው አመት ደግሞ፣ ከክፍሉ አንደኛ ወጣ። ከዚያም ከትምህርት ቤቱ አንደኛ በመሆን ተሸለመ። የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ሲያጠናቅቅ በመላ አሜሪካ ከፍተኛ ውጤት የሚያስመዘግቡ ተማሪዎችን አወዳድሮ ወደሚቀበለው ሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ገባ - በከፍተኛ ውጤት ነፃ የትምህርት እድል ተሰጥቶት። በቃ፤ የሚያቆመው አልተገኘም። ጆን ሆፕኪንስ ዩኒቨርስቲ ገብቶ፣ የአንጎል ቀዶ ህክምናን በማጥናት ተመረቀ። በሳይንሳዊ ጥናቶች ዙሪያ፣ ጆን ሆፕኪንስ ዩኒቨርስቲን የሚስተካከል የትምህርት ተቋም በአለማችን የለም። 33 የዩኒቨርስቲው ተመራቂዎችና አስተማሪዎች የኖቤል ተሸላሚ ሆነዋል። በዚህ ዩኒቨርስቲ ተምሮ መመረቅ ራሱ፣ ለካርሰን ትልቅ ስኬት ነው።

ግን አልበቃውም። በየአመቱ ከሶስት መቶ በላይ ከባድ የቀዶ ህክምና አገልግሎት በመስጠት የብዙ ሰዎችን ህይወት አድኗል። ይህም ብቻ አይደለም። በህፃናት የአንጎል ህክምና ላይ፣ መፍትሄ ላልነበራቸው በሽታዎች አዳዲስ የህክምና ዘዴዎችን በመፍጠር በመላው አለም በቀዳሚነት የሚጠቀስ ታላቅ ሰው ለመሆን በቅቷል - ዶ/ር ቤን ካርሰን። ሰዎች በራሳቸው ጥረት፣ ከ“ደደብነት” ወደ እውቀት ማማ መምጠቅ፣ በእውቀታቸውም ከድህነት ወደ ብልፅግና መሸጋገር እንደሚችሉ ይጠረጠራል? በቤን ካርሰን የጀግንነት ታሪክ ውስጥኮ ቁልጭ ብሎ ይታያል። አርአያነቱ፣ ለሁላችንም ነው። እውቀትን እየጨበጡ ወደ ስኬት መጓዝ ይቻላል። እስካሁን በጥበበኛ ሰዎች ጥረት የተገኙ አስደናቂ እውቀቶችን በስፋት መቅሰም የምንችለው ከመፃህፍት ነው። አዳዲስ እውቀቶችን ለመጨበጥ የሚያስችሉ ሳይንሳዊ ዘዴዎችንም ከመፃህፍት ውስጥ እናገኛለን። ያኔ፣ እንደ እውቀታችን መጠን እየሰራን ስኬትን እናጣጥማለን - በቃ… የጥረት ጉዳይ ነው፤ የንባብን ፍቅር የማዳበር ጉዳይ ነው። በእርግጥ፣ ሁሉም ሰው እንደ ልብ ጥሩ ጥሩ መፃህፍት ያገኛል ማለት አይደለም። የምንፈልገው አይነት መፅሃፍ ማግኘት… ለብዙዎች ብርቅ ነበር - እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ።

ኢትዮጵያ ውስጥ ቤተመፃህፍት ያላቸው ከተሞች ስንት ቢሆኑ ነው? እነሱም ቢሆኑ፣ የያዙት የመፃህፍት አይነትና ብዛት ቢቆጠር ኢምንት ነው። ዛሬ ግን፣ ያ ሁሉ “የመፅሃፍ ችጋር” ተረት እየሆነ ነው። የ“ኮፒ ራይት” ጥያቄ አነጋጋሪ ቢሆንም፣ በየትኛውም የእውቀት መስክ፣ በየትኛውም የእውቀት ደረጃ… ማማረጥ እስኪቸግረን ድረስ እልፍ መፃህፍት ማግኘት እንችላለን - በኢንተርኔት። ዛሬ፣ በመፃህፍት እጥረት ማሳበብ አይቻልም። የእውቀትና የስኬት በር፣ እዚሁ አጠገባችን መጥቷል። አንኳኩቶ መክፈትና መግባት ነው የኛ ድርሻ። በሩ ኮምፒዩተር ነው። ኢንተርኔትን በመጠቀም እናንኳኳ። መክፈቻው፣ የ“እንግሊዝኛ” ቋንቋ ነው። አብዛኞቹ መፃህፍት በእንግሊዝኛ የተዘጋጁ ናቸውና።

ከክርስቶስ ልደት በፊት በሶስተኛው ክፍለ ዘመን የነበረ ኩንግ ሲ የተባለ አንድ ንጉስ በቻይና ይኖር ነበር፡፡ ንጉስ አሳ በጣም ይወድ የነበረ መሪ ነበር ይባላል፡፡ የአገሩ ህዝብ በሞላ አሳ ይገዛና እጅ መንሻ ያቀርብለታል፡፡ ንጉሱ ኩንግ ሲዩ ግን ስጦታውን አልቀበልም፤ይላል፡፡ ይህንን ያየው ታናሽ ወንድሙ ወደ ንጉሱ ይመጣና “ያለጥርጥር አሳ በጣም እንደምትወድ አውቃለሁ፡፡

ስለምን ነው የአሳ ስጦታቸውን አልቀበልም ያልከው?” ሲል ጠየቀው፡፡ ንጉሱም፤ “ወንድሜ ሆይ ! የአሳ ስጦታ የማልቀበልበት ምክንያት፤ እያንዳንዱ ስጦታ በውለታ እንድትታሰር ያደርግሃልና ነው፡፡ በውለታ ከታሰርኩኝ የሃገራችንን ህግ እስከመጠምዘዝ ድረስ እሄዳለሁ፡፡” “ለምን ትጠመዝዛለህ?” “ውለታ የዋልክለት ህዝብ በፋንታው ይሄን አድርግ ብሎ ስለሚጠቨቅህ ነዋ!” “ለምን እምቢ አትልም ታዲያ?” “አሳ የምወድደወው ጭንቅላቴን ረቂቅ ስለሚያደርግልኝ ነው፡፡

ይሄንን እንዳረግ ያደረገኝም አሳ ነው!” “አልገባኝም” “አሳ አትበላማ! አሳ ሳትበላ እንዴት ይግባህ?” “ህጉ ቢጣመም ምን ቸገረህ? ስልጣኑ ያንተ?” “ህጉን ካጣመምኩ ራሴ ተጣምሜ ከስልጣኔ እወርዳለሁ” “ከስልጣንህ ብትወርድ ምን ቸገረህ?” “ከስልጣኔ ከወረድኩ በኋላ ራሴን አሳ ለመመገብ አልችል ይሆናል! በተቃራኒው ካየኸው ግን፤ከህዝብ የአሳ ስጦታ ባልቀበል፣ ከመንበሬ ባልወርድ፣ መቼም ቢሆን አሳ ገዝቼ መብላት አያቅተኝም!!”

                                                    * * *

ስጦታና እጅ መንሻ ስርዓትን እስከመናድ እንደሚደርስ በሀገራችን አይተናል፡፡ ከፈረንሳይ ድረስ የ70,000(ሰባ ሺ) ብር ሽቶ (ብራችን በዶላር 2.05 ብር ይመነዘር በነበረ ጊዜ) ለልደታቸው ስጦታ ይመጣላቸው የነበሩ ልዕልቶች እንደነበሩ ታዝበናል፡፡ የሀገር መሪዎች በስዊስ ባንክ አያሌ ሚሊዎን ብርና ወርቅ አስቀምጠው የነበረበት ወቅት እንደነበር አንረሳም፡፡ ይህን ዓይነቱ ነገር የዛሬ ስሙ ሙስና ነው፡፡ መታያ፣እጅ -መንሻ፣ስጦታ ፣የደስ ደስ ፣ቤት ማሞቂያ፣ህንፃ ማድመቂያ፣እጅ ማበሻ… ሁሉም የሙስና ተለዋጭ ስሞች ናቸው፡፡ “ሙሳዊ ጫና የክፉ ስራዎች ሁሉ የዓመት ከዓመት ፀደይ ነው፡፡

የስርዓቱ ብልሽት መጠንሰሻ ነው፡፡ የአገር ዕዳ ክምር - ክንብንብ ነው፡፡ ክንዳችንን ያልማል፡፡ ከሸንጎ ውስጥ የጥበብን ብልት ቆርጦ ስልጣንን ለግል ጥቅም ለማዋልና ስምና ዝናን ማትረፊያ ለማድረግ እንድናውለው ያመቻችልናል!” ይለናል በርክ የተባለው ፀሐፊ፡፡ ይህሁነት በዲሞክራሲ ማነቆነት፣ በልማት እንቅፋትነት፣ በሃይማኖት ግጭት መንስዔነት፣ በጦርነት ሰበብነት ትልቅ ተፅዕኖ ቢፈጠር ዞሮ ዞሮ ጦሱ ለሀገር ነው የሚተርፈው፡፡ ጀርመኖች ደግሞ ስለታላላቅ ጦርነቶች የሚከተለውን ይላሉ፡- ታላቅ ጦርነት ሃገሪቱን የሶሰት ዓይነት ሰራዊት ባለቤት ያደርጋታል፡- የጦር- ጉዳተኞች ሰራዊት፣ የሐዘንተኞች ሰራዊት እና የሌቦች ሰራዊት! ሃይማኖቶች የቅዱሳት፣የቀና መንፈስ፣የመልካም ስራ መመሪያ የሚሰጡ፣የበጎ ምግባር አቅጣጫ መሪ እንጂ የግጭት መንስኤና ሰበብ መሆን የለባቸውም፡፡ ለዚህ ነው:- “ሃይማኖት ታረደ ደሙን ኩቲ ላሰው እንግዲህ ሆድ ለሆድ አልተገናኘም ሰው” እያለ የሀገራችን ሰው የሚገጥመው፡፡

ሁሌ የምንሰራው ስራና የእንቅስቃሴያችን ሂደት “በተሳካ ሁኔታ መጠናቀቁ ተገለፀ”፣ “የስራ ግምገማው እንደሚያሳየው የዕድገት አቅጣጫ ጠቋሚ ነው”፤ “በይሄን ያህል ፐርሰንት ያደግን መሆኑ ተገለፀ” ወዘተ እየተባባልን ችግሮቻችንን እንዳናይ ዐይናችንን መጨፈን ትልቅ አባዜ ነው፡፡ “ሞኝ፤የሚያደንቀው ሞኝ አያጣም”፤ እንዲሉ እርስ በርስ በመደናነቅና “አበጀህ”፣ “አበጀህ!” በመባባል ብዙ የተራመድን በመሰለን ጊዜ መስጋትና መጠንቀቅ ብልህነት ነው፡፡ ፍትህ፤ ዕውነታችን በየትኛው አቅጣጫ እንዲበራ እንደምናደርግ ራሳችንን የምንፈትሽበት ድንቅ መሳሪያ ነው፡፡ “ስለ አገርህ፣ስለ አምላክህ፣ስለ ዕውነትህ፤ ይሁን እንጂ ቅን ዓላማህ፣ ፍትሐዊነት ቅን ፀጋ ነው፣ ፈፅሞ ፍርሃት አይግባህ” (ይላል ሼክስፒር) ዲሞክራሲያችንን እንፈትሽ፡፡ “ዲሞክራሲን ማፍቀር እኩልነትን ማፍቀር ነው፡፡”

ይለናል ሞንቴስኩ፡፡ ይህ የእኩልነት ፍቅር አለን ወይ? “ዲሞክራሲ ምርጥና ለመተግበር እጅግ አዳጋች የፖለቲካ አደረጃጀት ነው” ይለናል ራልፍ ባርተን፡፡ ይህንንስ ተገንዝበናል?(dynamic democracy) ተንቀሳቃሽ እና አንቀሳቃሽ ዲሞክራሲ ካልሆነ ዲሞክራሲ የለም ብንል ይሻላል፡፡ ህዝባችን መሳተፍ ሲያቆም፣ፀሀይ ውስጥ ቦታ ሲያጣ -ያኔ ሁላችንም በመበስበስ (በንትበት) ጨለማ (darkness of decadence)ውስጥ በነን እናልቃለን፡፡ ሁላችንም ዲዳ ፣ሞራለ - ቢስ እና የቀለጡ ነብሶች እንሆናለን” (ሳውል ደ-አሊንስኪ) ዲሞክራሲ ስንል እንደፕሉታርክ “ሂድ፡፡ በራስህ ቤት የራስህ ዓይነት ዲሞክራሲ ሞክር” ማለታችን ቢሆንም ይመረጣል፡፡ የሙስናን፣ የጎረቤትን የጦርነትን፣ የሃይማኖትን ነገር፣ የዲሞክራሲንና የዕድገትን ነገር፣ በወጉ ለማየት ችግራችንና መፈርትሄዎቻችንን በተያያዘ ጥምረት ማገናዘብ አለብን፡፡

የሃገራችንን ችግር ስንቃኝ አንዱን ካንዱ አስተሳስረን መሆን አለበት፡፡ አለበለዚያ የአንድ ሰሞን ግርግር ዘመቻ ብቻ ይሆናል፡፡ ተከታታይ ጥረትና ቀጣይነት አይኖረውም፡፡ አንዱን ዘመቻ ሌላው እያስረሳውና እየሻረው ስለሚሄድ ዕድገታችን ደብዛዛ ይሆናል፡፡ የተሳሰረ ጥረት የማይረሳሳ ትግል ነው ሊኖረን የሚገባው፡፡ በተበታተነ ሁኔታ ውስጥ እንዳንበታተን፤ አረሙን፣ እንቅፋቱን፣ ዳተኝነቱንና ግብዝነቱን ትተን፣ ለመጓዝ፤ ”የመጣ ሳይመጣ የውሃ ቦይ ጥረግ” የሚለውን ተረት ማሰብ አለብን!!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

        የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራር ዛሬ ግምገማ ያካሂዳል

የኢህአዴግ 36 ከፍተኛ መሪዎችን ያካተተው የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አመታዊ ግምገማ ለማካሄድ ዛሬ የሚሰበሰብ ሲሆን የስምንት ሚኒስትሮች ሹም ሽርና ሽግሽግ በሚቀጥለው ሳምንት ለፓርላማ ቀርቦ እንደሚፀድቅ ይጠበቃል፡፡ ለሹመት የሚቀርቡት ባለስልጣናት፤ የፍትህ ሚኒስትር፣ የከተማና ኮንስትራክሽን ልማት ሚኒስትር፣ የግብርና ሚኒስትር፣ የትራንስፖርት ሚኒስትር፣ የገቢዎች ሚኒስትር የደህንነትና መረጃ ሚኒስትር፣ የደንና አካባቢ ጥበቃ ሚኒስትር እንዲሁም በፓርላማ የመንግስት ተጠሪ ሚኒስትር ናቸው ተብሏል፡፡ አንዳንዶቹ ሹምሽር እርምጃዎች ሲሆኑ፤ አንዳንዶቹ ደግሞ ወደ አዲስ አበባ አስተዳደር እንዲዛወሩ በተደረጉ ባለስልጣናት ምትክ የሚካሄድ ሽግሽግ ነው፡፡

ይሁን እንጂ የእጩ ተሿሚዎችን ማንነት ለማወቅ ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም፡፡ ዛሬ የሚካሄደው የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ስብሰባ ከሹምሽሩ ጋር የተያያዘ እንደሆነ ቢታሰብም፣ የሰብስባው ዋና ርዕሰ ጉዳይ አመታዊ ግምገማና አመታዊ እቅድ እንደሆነ ተነግሯል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመሩት አስፈፃሚ አካል የመቆጣጠር ስልጣን ያለው የአገሪቱ ፓርላማ ጠንካራ የቁጥጥር ሃላፊነቱን በተግባር ማሳየት እንደጀመረ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጭምር ቢናገሩም፤ በሚኒስትሮች ሹመት ዙሪያ ግን የቀድሞው አሰራር አልተሻሻለም፡፡ በተለያዩ ዲሞክራሲያዊ አገራት ውስጥ የእጩ ሚኒስትሮች ማንነት በይፋ ታውቆ ለበርካታ ሳምንታት በፓርላማና በዜጐች ዘንድ ውይይት የሚካሄድበት ቢሆንም፣ በኢትዮጵያ ግን የተሿሚዎች ማንነት የሚገለፀው ሹመታቸው በሚፀድቅበት እለት ነው፡፡

የስራ አስፈፃሚው ኮሚቴ ዛሬ ስብሰባ እንደሚያካሂድ የገለፁት የኢህአዴግ ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ ሬድዋን ሁሴን፤ የስብሰባው ዓላማ የዓመቱን የስራ አፈፃፀም በመገምገም ድርጅቱ በኪራይ ሰብሳቢነት ላይ የሚያካሂደውን ትግል አጠናክሮ ለመቀጠል በእቅዶች ላይ መወያየት ነው ብለዋል፡፡ የህዝቡን ተጠቃሚነትና ተሳትፎ በማጐልበት የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከትን፤ የህዝብ፣ የመንግስትና የድርጅት አቋሞች እንዲጠናከሩ፣ ችግሮች ያሉባቸውን ደግሞ አንጥሮ ለማውጣት ያለመ ስብሰባ ነው ብለዋል፡፡ በነባር ፖሊሲዎችና አሰራሮች ላይ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴው መክሮባቸው አቋም ከወሰደባቸው በኋላ፤ የማስፋት፣ የማጠናከርና የማጐልበት እንዲሁም ተጨማሪና አዳዲስ ዝርዝር የአሰራር አቅጣጫዎችን በመተለም በመጪው አመት እቅድ ላይ ውሳኔ ያሳልፋል ብለዋል - አቶ ሬድዋን፡፡

Published in ዜና

የአዲስ አበባ የቤቶች ልማት የቁጠባ ፕሮግራም መንግስታዊ በሆነው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ብቻ እንዲከናወን መደረጉ በግል ባንኮች ላይ ከፍተኛ ኪሣራ እያስከተለ እንደሆነና በአጭር ጊዜ የግል ባንክ ዘርፉን ህልውና አደጋ ላይ እንደሚጥል የባንክ ባለሙያዎች ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡ እስካሁን ከ750ሺህ በላይ ግለሰቦች የቤቶች ልማት ቁጠባ ሂሣብ በንግድ ባንክ እንደከፈቱ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ አንድ የግል ባንክ ባለሙያ፤ እሣቸው በሚሠሩበት ባንክ ደንበኛ የነበሩ ግለሠቦች በቤቶች የቁጠባ ፕሮግራም ተሣታፊ ለመሆን ከባንኩ ገንዘብ በማውጣት በመንግስት ባንኮች እያስቀመጡ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡

ባለፉት ጥቂት ሣምንታትም ባንኩ በዚህ አገልግሎት ተጠምዶ መቆየቱን የተናገሩት ባለሙያው፤ “በእነዚህ ጊዜያትም የባንክ ሂሣብ ለመክፈት ወደ ባንካችን የመጣ ደንበኛ አላጋጠመኝም” ብለዋል፡፡ በባንኩ ያላቸውን ገንዘብ ለማውጣት የሚመጡ ደንበኞች መበራከታቸውንና ይህም ባንኩ ራሱን ለማቋቋም ለዓመታት የደከመበትን ልፋቱ ከንቱ እንደሚያስቀረውና ቀጣይ ህልውናውንም አደጋ ላይ እንደሚጥለው ባለሙያው ይናገራሉ፡፡ ስማቸውና የሚሠሩበት ባንክ እንዲገለፅ ያልፈለጉ ሌላ ባለሙያም፤ በአሁን ሠአት ባንካቸው የውጭ ምንዛሬ እና የሃዋላ አገልግሎቶችን ከመስጠት ባለፈ አዳዲስ የባንክ ሂሣብ የሚከፍቱ ደንበኞች እያስተናገደ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡ ሁኔታው በዚህ ከቀጠለም የባንኩ ህልውና አደጋ ላይ እንደሚወድቅ ስጋታቸውን ገልፀዋል፡፡

የኢዴፓ ሊ/መንበርና ከፍተኛ የባንክ ባለሙያ የሆኑት አቶ ሙሼ ሠሙ በበኩላቸው፤ መንግስት መንግስታዊ በሆነው የንግድ ባንክ በኩል ብቻ ዜጐች እንዲቆጥቡ ማወጁ ከነፃ ገበያ ስርአት ጋር የሚቃረን መሆኑን ገልፀው ይህና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች በግል ባንኮች ላይ ከፍተኛ የህልውና አደጋ መጋረጣቸውን ተናግረዋል፡፡ በዚህ አካሄድ ከቀጠለም ያለ ጥርጥር ከሶስት እና አራት አመታት በኋላ የበርካታ የግል ባንኮች ህልውና እስከ መጨረሻው ሊያከትም ይችላል ብለዋል - አቶ ሙሼ፡፡ የቤቶች ልማት ቁጠባ ፕሮግራም ሁለት መሠረታዊ ተፅዕኖዎች አሉት የሚሉት አቶ ሙሼ፤ አንደኛው በግል ባንክ ውስጥ ከሚያስቀምጡ ደንበኞች ገንዘብ ላይ ማበደር አንዱ የባንኮች ተግባር መሆኑን ገልፀው፤ አሁን ግን ይህን ተግባር የሚያከናውኑበት ገንዘብ ወደ መንግስታዊ ባንክ እንዲሸሽ መደረጉን ይናገራሉ፡፡

ይሄም ብቻ ሳይሆን የግል ባንኮች በብዙ ዓመታት ያፈሯቸውን ነባር ደንበኞችም እንዲያጡ ያደርጋል ብለዋል፡፡ መንግስት የቀረፀው የቤቶች ልማት ፕሮግራም የግል ባንኮች አዳዲስ ደንበኞችን እንዳያፈሩ ማድረጉ ሁለተኛው ተፅዕኖ ነው የሚሉት ባለሙያው፤ በተቃራኒው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከአንድ ሚሊዮን በላይ አዲዲስ ደንበኞችን እንዲያገኝ ይረዳዋል ብለዋል፡፡ ነባሩም ይሁን አዲስ ደንበኛ ከግል ባንኮች ወጥቶ ወደ መንግስት ባንክ መሄዱ የነፃ ገበያ ስርአት እንዲከስም ከማድረጉ ባሻገር ባንኮችም በህብረተሠቡ ዘንድ ለዘመናት የገነቡትን ጠንካራ እምነት እንዲያጡ ያደርጋል በማለት የግል ባንኮች ላይ የተጋረጠውን አደጋ ባለሙያው አስረድተዋል፡፡ መንግስት የግል ባንኮች ከሚያበድሩት ገንዘብ ላይ 27 በመቶ የህዳሴውን ግድብ ቦንድ እንዲገዙ ማዘዙን ያስታወሡት አቶ ሙሼ፤ የአሁኑ የግል ባንኮችን ያገለለው የቤቶች ቁጠባ ፕሮግራም ሲጨመርበት በባንኮቹ ላይ የሚደርሰው ጉዳት የቱን ያህል እንደሆነ መገመት አያዳግትም ብለዋል፡፡ “መንግስት የግል ባንኮችን ለማጥፋት ታጥቆ መነሣቱ የሚገርመኝ ጉዳይ ነው” ያሉት አቶ ሙሼ፤ በዚህ አካሄድ ከሦስት እና አራት አመት በኋላ የግል ባንኮች ሊጠፉ እንደሚችሉ ምንም ጥያቄ የሚያስነሣ ጉዳይ አይደለም ይላሉ፡፡

ኢህአዴግ ጉልበትና አቅም ያለው የግል ዘርፍ እንዲፈጠር አይፈልግም የሚሉት አቶ ሙሼ፤ በግል ባንኮች ላይ እየደረሠ ያለው ጫናም የዚሁ መገለጫ ነው ብለዋል፡፡ ለዚህ አባባላቸው ማስረጃ ሲያቀርቡም በቅርቡ የወጣ ጥናት ኢትዮጵያ በመንግስት ኢንቨስትመንት ከአለም 2ኛ ደረጃ ላይ ስትቀመጥ በግል ኢንቨስትመንት ግን በመጨረሻው ረድፍ ከተዘረዘሩት ሃገራት አንዷ ነች ብለዋል፡፡ አቶ ቡልቻ ደመቅሣ በበኩላቸው፤ ከዚህ በፊትም ከቻይና ለሚመጣ ማንኛውም እቃ በንግድ ባንክ በኩል ብቻ ግብይቱ ይፈፀም የሚል ህግ መፅደቁን አስታውሠው፣ ያሁኑ ሲጨመርበት በእርግጥም የግል ባንክ ዘርፉ ከፍተኛ አደጋ ተጋርጦበታል ብለዋል፡፡ መንግስት በተደጋጋሚ በባንክ አሠራር ውስጥ ጣልቃ መግባቱ ለዘለቄታው የማያዋጣ ተግባር መሆኑን የጠቆሙት አቶ ቡልቻ፤ እንዲህ ማድረጉም አገሪቱን የዓለም ንግድ ድርጅትን ከመሳሰሉ ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ማህበራት አባልነት እንዳገለላት በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

ምርመራው እየተጠናቀቀ ነው ብሎ እንደሚያምን ፍ/ቤቱ ገልጿል

የገቢዎችና ጉምሩክ መስሪያ ቤትን በሚኒስትር ማዕረግ የሚመሩ ዳሬክተርና ምክትላቸውን ጨምሮ በርካታ ስራ አስኪያጆችና የስራ ኃላፊዎች በተጠርጣሪነት የታሰሩበት የሙስና ምርመራ በዚህ ሳምንት እንደገና እንዲራዘም ፍ/ቤት ፈቅዷል፡፡ ቢሆንም ምርመራው መቋጫ እንዲኖረው ማሳሰቢያ አዘል ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ ምርመራውን በትጋት እያካሄደ መሆኑን የገለፀው የፀረ ሙስና ኮሚሽን፤ ተጨማሪ ጊዜ እንደሚያስፈልገው በመግለጽ ለአራተኛ ጊዜ ቀጠሮ እንዲራዘምለት የጠየቀ ሲሆን የታሳሪ ጠበቆች በበኩላቸው፤ የኮሚሽኑ ምርመራ እልባት የሚያገኘው መቼ ነው ሲሉ ተቃውሟቸውን አሰምተዋል፡፡ ሰሞኑን ፍ/ቤት ቀጠሮ የነበራቸውም በአምስት መዝገቦች ምርመራ የሚካሄድባቸው 37 ተጠርጣሪዎች ሲሆኑ ሦስቱ በዋስ ተለቀዋል፡፡

የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ምክትል ዳሬክተር አቶ ገ/ዋህድንና ባለቤታቸውን ጨምሮ 11 ተጠርጣሪዎች የተካተቱበት የምርመራ መዝገብ ባለፈው ሰኞ እለት በፍ/ቤት የታየ ሲሆን፣ የአቶ ገ/ዋህድ ባለቤት ኮሎኔል ሃይማኖት ተስፋዬ የዋስ ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ የልጆች እናት እንደሆኑና ልጆቻቸው ትምህርታቸውን ለመከታተል እንደተቸገሩ ለፍርድ ቤቱ የገለፁት ኮ/ል ሃይማኖት፤ በዋስ ከእስር ወጥተው ጉዳያቸውን ለመከታተል እንዲፈቀድላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፀረ ሙስና ኮሚሽን ተቃውሞውን ሲያሰማ፣ ኮ/ል ሃይማኖት ቀደም ሲል ሰነድ በማሸሽ ከመጠርጠራቸውም በተጨማሪ፣ “ሞኒት” በተሰኘ ኩባንያ ተቀጥረው የባለቤታቸውን ስልጣን ተገን በማድረግ ግብር የመሰወር ተግባር ፈጽመዋል ተብለው እንደተጠረጠሩ ገልጿል፡፡ ፍ/ቤቱ የኮ/ል ሃይማኖትን የዋስትና ጥያቄ ሳይቀበለው ቢቀርም፣ ከሌላ የምርመራ መዝገብ ጋር በተያያዘ የታሰሩ ሦስት ተጠርጣሪዎች በዋስ ተለቀዋል፡፡

ማክሰኞ ሰኔ 18 ቀን በሚኒስትር ማዕረግ የገቢዎችና የጉምሩክ ባለስልጣን ዳሬክተር የነበሩ አቶ መላኩ ፋንታን ጨምሮ 11 ተጠርጣሪዎች በተያዙበት የምርመራ መዝገብ ፍ/ቤት ቀርቧል፡፡ አቶ መርክነህ አለማየሁ 1.3 ሚ. ብር ለመደበቅና ለመቅበር ሲሞክሩ ተባብረዋል የተባሉ ወንድማቸው አቶ ብርሃኑ አለማየሁ እና ዘመዳቸው አቶ ገተፎ መታሰራቸው የሚታወስ ሲሆን በዋስ ተለቀዋል፡፡ ረቡዕ ሰኔ 19 ቀን ደግሞ አቶ ጥጋቡ ግደይ ጨምሮ፤ 5 ተጠርጣሪዎችን የያዘው መዝገብ ፍ/ቤት ሲቀርብ ወ/ሮ ሶፊያ ሱሌማን የዋስ ጥያቄ አቅርበው የፀረ ሙስና ኮሚሽን ተቃውሞ እንደሌለው በመግለፁ በ2ሺ ብር ዋስ ተለቀዋል፡፡ ከሰኞ እስከ ሐሙስ ድረስ በፍ/ቤት የተመለከታቸው አምስት የምርመራ መዝገቦች ላይ ዋናው አከራካሪ ጉዳይ የነበረው ግን የጊዜ ቀጠሮ ጉዳይ ነው፡፡

ሦስቴ የ14 የጊዜ ቀጠሮ እያስፈቀደ ምርመራ ሲያካሂድ የቆየው የፀረ ሙስና ኮሚሽን፤ ያከናወናቸውንና ቀሪ ስራዎችን በመዘርዘር ተጨማሪ የሁለት ሳምንት ቀጠሮ ጠይቋል፡፡ የተጠርጣሪዎች ጠበቆች በበኩላቸው፤ የፀረ ሙስና ኮሚሽን ለ4ኛ ጊዜ የ14 ቀን ቀጠሮ መጠየቁ፣ ተጠርጣሪዎች ያለ በቂ ማስረጃ እንደታሰሩ ያሳያል ብለዋል፡፡ ተጠርጣሪዎች ክስ ሳይመሰረትባቸው ለ45 ቀናት መታሰራቸው ተገቢ አይደለም በማለት የተከራከሩት ጠበቆች፣ እየተጓተተ የመጣው ምርመራ ማብቂያው የት ነው ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ የፀረ ሙስና ኮሚሽኑ ስራውን በትጋት እንዲሰሩ ፍ/ቤት ትዕዛዝ ይስጥልን ሲሉም አቤቱታ አቅርበዋል፡፡

ፀረ ሙስና ኮሚሽን በትጋት እየሰራ መሆኑን በመጥቀስ በሰጠው ምላሽ፣ ምርመራው ሠፊና ውስብስብ በመሆኑ ጊዜ ያስፈልገዋል ብለዋል፡፡ ፍ/ቤቱ የግራ ቀኙን ክርክር ከተመለከተ በኋላ፣ ምርመራው በአብዛኛው እንደተከናወነ መገንዘቡን ጠቅሶ፤ ከምርመራው ውስብስብነትና ስፋት አንፃር ለቀሪ ስራዎች የጊዜ ቀጠሮ መፍቀዱን ገልጿል፡፡ ነገር ግን ለፀረ ሙስና ኮሚሽን ምርመራውን እንዲቋጭ የሚገፋፋ ማሳሰቢያ አዘል ትዕዛዝ ፍ/ቤቱ ሰጥቷል፡፡ ፀረ ሙስና ኮሚሽን በቀጣይ ቀጠሮ በእያንዳንዱ ተጠርጣሪ ላይ ምን ያህል የሰነድና የምስክር ቃል እንዳዘጋጀ በግልጽ ዘርዝሮ እንዲያቀርብ በፍ/ቤቱ ታዟል፡፡

Published in ዜና

ዜጐች ራሣቸው ሊሠሩት በሚገባው የቤቶች ልማት ፕሮግራም ውስጥ መንግስት መግባቱ ተገቢ አለመሆኑን የተናገሩ ተቃዋሚ ፓርቲዎች፤ ከአገሪቱ አቅም አንፃር ፕሮግራሙ በተባለው ጊዜ ውስጥ ተፈፃሚ ይሆናል የሚል እምነት እንደሌላቸውም ገለፁ፡፡ የባንክ ባለሙያ የሆኑት የኢዴፓ ሊቀመንበር አቶ ሙሼ ሠሙ፤ ማንኛውም ዜጋ ቤት ማግኘት ያለበት በራሱ ጥረት እንጂ እንደ ሎተሪ እጣ እየወጣለት አይደለም ብለዋል፡፡ መንግስት በማይመለከተው ተግባር ላይ መሠማራቱን የጠቀሱት አቶ ሙሼ፤ ፕሮግራሙን ለማስፈፀም የሚውል ፈንድ ለማግኘት ገንዘብ ካላተመ በስተቀር አቅም እንደሌውም ተናግረዋል፡፡

የቤት ግንባታውን ለማከናወን በሚሊዮን የሚቆጠር የሠው ሃይል እንደሚያስፈልግ በመጠቆምም እነዚህ ሁሉ ተደማምረው የተባለው የቤት ፕሮግራም በተባለው ጊዜ ይሣካል የሚል ግምት እንደሌላቸው ገልፀዋል፡፡ የፓርላማ አባልና የአንድነት ፓርቲ ምክትል ሊቀ መንበር አቶ ግርማ ሠይፉ በበኩላቸው፤ መንግስት የዜጐች ቤት ሠሪ ሊሆን እንደማይገባውና ከዚያ ይልቅ ለግለሠቦች ሁኔታውን አመቻችቶ እንዲሰሩ ማድረግ እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ የቤት ልማት ፕሮግራም የተባለው ነገር ትርጉም የማይሠጥ ነው ያሉት አቶ ግርማ፤ መንግስት ይህን እቅድ የዘረጋው የቁጠባ ባህልን ለማሣደግ እንደሆነ ጠቁመው፤ እንደተባለው ሁሉም ተመዝጋቢ የቤት ባለቤት ይሆናል ብለው እንደማያምኑ ገልፀዋል፡፡ የፖለቲካ ሣይንስ ምሁሩ እና የመድረክ አመራር አባል ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ የቤት ፕሮግራም ተብሎ የተቀመጠው ቢሣካ ጥሩ እንደነበር ገልፀው፤ ነገር ግን መንግስት ብዙ ድስቶችን ጥዶ የሚንቀሣቀስ በመሆኑ የመሣካት እድል ያለው አይመስለኝም ብለዋል፡፡

ዶ/ር መረራ ግርማ በማከልም ፕሮግራሙ የፖለቲካ ጨዋታ ያለበትና በዋናነት ቀጣዩን ምርጫ ታሣቢ ያደረገ እንደሚመስላቸው ገልፀዋል፡፡ ለረጅም አመታት በተለያዩ አለማቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ውስጥ የሠሩት የመድረክ አመራር አቶ ቡልቻ ደመቅሣ በበኩላቸው፤ መንግስት የዘረጋውን የቤት ልማት ፕሮግራም አጥብቀው እንደሚቃወሙ ገልፀው፤ መንግስት በነጋዴ ሥራ ውስጥ እየገባ ነው ብለዋል፡፡ “መንግስት ነጋዴ እንዲሆን አይደለም የሚመረጠው፤ የሃገር ሉአላዊነትን እንዲጠብቅ፣ ፍትህን እንዲያሠፍን እና ግብር እንዲሠበስብ እንጂ” ሲሉ የመንግስትን ሚና አስረድተዋል፡፡

Published in ዜና

       ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታው ተጠናቆ በሙሉ አቅሙ ስራ ሲጀምር ለመቶ አመታት በየቀኑ 2 ሚሊዮን ዩሮ ከኤሌክትሪክ ሽያጭ እንደሚያስገባ ተገለፀ፡፡ ገቢው የኢትዮጵያዊያንን ህይወትና ኢኮኖሚ መልክ ይቀይራልም ተብሏል፡፡ ትላንት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ላይ ማንዴላ የስብሰባ አዳራሽ በተካሄደው ሲምፖዚየም ላይ በቀረበው ጥናት፤ ግድቡ በየቀኑ የተጠቀሰውን ያህል ገቢ ከማስገኘቱም በላይ በጎርፍ አደጋ የሚጠቁትን እነ ሱዳንን ከጎርፍ አደጋና ከድርቅ ይታደጋል ተብሏል፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የውሃ ሃብት ኢንስቲትዩት ምሁር ዶ/ር ይልማ ስለሺ፤ “Nile Hydrology and Ethiopian Dams, Great Ethiopian Renaissance Dam - a case study” በሚል ርዕስ ለሲምፖዚየሙ ተሳታፊዎች ባቀረቡት ጥናት፤ የግድቡ መገንባት ከኢትዮጵያ ሌላ ለሱዳንና ለግብፅ እንዲሁም ለአለም ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ገልፀው፤ በተለይ ሱዳን ስትቸገር ለኖረችበት የጎርፍ አደጋ ፍቱን መፍትሄ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡ የህዳሴው ግድብ ጎርፍንና ፍሰቱን በመቆጣጠር ከአደጋ ከመከላከሉም በላይ 74 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ ውሃ በማጠራቀም፣ ሱዳንና ግብፅ በድርቅ ወራት ሊመጣባቸው ከሚችለው የውሃ ችግር ራሳቸውን ለማዳን ያስችላቸዋል ተብሏል፡፡

ግድቡ ካሉት ጠቀሜታዎች መካከል በየአመቱ በትነት የሚባክነውን ውሃ መቆጠብ አንዱ ሲሆን ድርቅን ለመቋቋም፣ አዲስ የሀይል እድሎችን ለመጠቀም፣ ደለልን ለመቆጣጠርና መሰል ጥቅሞች እንዳሉት ተጠቁሟል፡፡ ግድቡ ከድንጋይ ከሰልና ከነዳጅ የሚለቀቀውን በካይ ጋዝ በመቀነስ የአለምን የሙቀት መጠን (global warming) ለማስተካከል ትልቅ ሚና እንዳለውም ተገልጿል፡፡ በሲምፖዚየሙ ወደ አምስት የሚጠጉ አባይን እና ታላቁን የህዳሴ ግድብ የተመለከቱ ጥናቶች ቀርበው ውይይት የተደረገባቸው ሲሆን አንድ ምሁር ሲምፖዚየሙን አስመልክተው ሲናገሩ፤ “የዛሬው ሲምፖዚየም የኢትዮጵያ፣ የሱዳንና የግብፅ መንግስታት በቅርበት በመወያየትና ለችግሮቻቸው እልባት በመስጠት ወደፊት የሚራመዱበትን አቅጣጫ ለመወሠን ይረዳቸዋል” ብለዋል፡፡

በሲምፖዚየሙ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩን አቶ አለማየሁ ተገኑን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት፣አምባሳደሮች፣ባለድርሻ አካላትና የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ተሳትፈዋል፡፡ በሲምፖዚየሙ የተሳተፉት ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ፤ “ጥናቱ ቴክኒካል ቢሆንም ብዙ እንድናውቅ እና አንድ አቋም ስንወስድ በእውቀትና በመረጃ የተደገፈ እንዲሆን ይረዳናል” ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የሰላምና የልማት ኢኒስትትዩት ዋና ዳሬክተር አቶ ስብሃት ነጋም፤ ጥናቱ እጅግ አስተማሪ መሆኑን ጠቁመው፤ በአማርኛም ተተርጉሞ ቢሰራጭና ሁሉም ቢያውቀው ጠቃሚ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና
Page 3 of 17