ሰላም ሰፍኖ አገሬ ስመለሰ እዚህ በቀሰምኩት የጥልፍና የልብስ ስፌት ሙያ ቤተሰቤን አስተዳድራለሁ፤ ሙያውንም ለሌሎች አስተምራለሁ ትላለች በባምባሲ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ በስፌት መኪና ጥልፍ ስትሠራ ያገኘናት ሱራ አደም ኢብራሂም፡፡ የተበደለና የተገፋ ሰው ወደ ሌላ ስፍራ ተዛውሮ ጥሩ ነገር ሲገጥመው፣ “የልምጭም ገድ አለው” ይላል የአገሬ ሰው፡፡ ሱራ፣ የጊዘን-ሱዳን አካባቢ ነዋሪ ነበረች፡፡ እዚያ እያለች የስፌትና የጥልፍ ሙያ ቀርቶ ቋሚ መተዳደሪያ እንኳ አልነበራትም። እሷና ጐረቤቶቿ የማገዶ እንጨት ለቃቅመውና ለውዝ (ኦቾሎኒ) ገበያ ወስደው በመሸጥ ነበር የሚተዳደሩት፡፡

አሁን ግን በባምባሲ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ በልብስ ስፌትና በጥልፍ ሙያ ለአምስት ወራት ሠልጥና እየሠራች ነው፡፡ የባምባሲ ስደተኞች ጣቢያ በፕላን የተሠራ የጎጆ ቤቶች መንደር ነው፡፡ በገላጣ ቦታ የተሠራው ጣቢያ ከፍ ካለ ስፍራ ሲታይ፣ የመንገዶቹ ቅያስ፣ የቤቶቹ በረድፍ መደርደር … ዓይን ከመማረኩም በላይ ዘመናዊ ከተማ ይመስላል፡፡ ከሱዳን ድንበር 120 ኪ.ሜ ላይ የተሠራው ጣቢያ፣ ሦስት ዞኖች፣ 40 ብሎኮች፣ 265 ቤቶችና 5240 አባ/እማወራዎች ሲኖሩት በአጠቃላይ 12,338 የሱዳን ተፈናቃዮችን ይዟል፡፡ በ2004 ዓ.ም መጀመሪያ ላይ በሱዳን ብሉ ናይል ግዛት በተፈጠረ ያለመረጋጋት ከመኖሪያቸው ለቅቀው ወደ ኢትዮጵያ የገቡ የሱዳን ስደተኞችን በተለያዩ የመግቢያ በሮች፣ በባምዛ፣ በኩርሙክ፣ በገመድና በሸሸቆ ሲገቡ በመቀበል፣ በማጓጓዝና በመጠለያ ጣቢያዎች ለማስፈርና አስፈላጊውን ሰብአዊና አካላዊ ጥበቃ በማድረግ ኢትዮጵያ የፈረመቻቸውን ዓለም አቀፍና አኅጉራዊ ስምምነቶች ተግባራዊ በማድረግ ላይ ነን ያሉት የስደተኞችና ከስደት ተመላሾች ጉዳይ አስተዳደር፣ የአሶሳ ስደተኞች ፕሮግራም ማስተባበሪያ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ሞላ እጅጉ ናቸው፡፡ አቶ ሞላ አክለውም፣ በሦስት መጠለያ ጣቢያዎች፣ ከ15 ዓመት በፊት በተሠራው በሸርቆሌ፣ በኅዳር ወር በተሠራው በቶንጉና የዛሬ ዓመት በሰኔ ወር በተሠራው በባምባሲ መጠለያ ጣቢያዎች በአጠቃላይ ከ32,263 በላይ ስደተኞች እንደተጠለሉና በአሁኑ ወቅትም በሳምንት በአማካይ ከ20 እስከ 30 ስደተኞች ድንበር አቋርጠው ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ መሆኑን፣ እንዲሁም በአሁኑ ወቅት ሦስቱም መጠለያ ጣቢያዎች ስለሞሉና የስደተኞችም ፍልሰት ስላላቆመ፣ አራተኛ ጣቢያ በጉሬ ለማቋቋም እየተዘጋጁ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የዛሬ ዓመት የባምባሲ መጠለያ ጣቢያ ሲከፈት ለመጀመሪያ ጊዜ የተቀበሉት የስደተኞች ቁጥር 400 እንደነበር፣ በአሁኑ ወቅት ግን ቁጥራቸው ከ12ሺህ በላይ መሆኑን የጣቢያው አስተባባሪ አቶ ተስፋዬ ጣፋ ገልጸዋል፡፡

በጣቢያው፣ በኢትዮጵያ መንግሥት ጋባዥነት ስምንት ዓለም አቀፍና አገር በቀል ድርጅቶች በውሃ አቅርቦት፣ በሥነ ፆታ ትምህርትና ጥቃት ዙሪያ፣ በመዋለሕፃናት ትምህርትና በሕፃናት በሽታ መከላከል፣ በመፀዳጃ ቤት አቅርቦት፣ በአካባቢ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ፣ ስደተኞችን ከመግቢያ በሮች ተቀብሎ ወደ መጠለያዎች ማጓጓዝና በመጠለያ ቤት ሥራ፣ በስደተኞች አካላዊ ጥበቃና እንክብካቤ፣ በመሠረታዊ የጤና አገልግሎትና በሥነ-ምግብ አቅርቦት… ዙሪያ ለስደተኞች አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸውን አቶ ተስፋዬ አስረድተዋል፡፡ ዶ/ር ሙሉጌታ ተድላ፤ የባምባሲ ስደተኞች መጠለያ ጣቢያ ሜዲካል ዳይሬክተር ናቸው፡፡ ጣቢያው 16 የሕክምና ቡድን አባላት እንዳለው ጠቅሰው፤ ሥራቸውም አገሪቷ በምትከተለው ፖሊስ መሠረት በመከላከል ላይ ያተኮረ መሆኑን ገልጸዋል። መደበኛ የክትባት አገልግሎት ባለፉት ሁለት ወራት በስፋት የተሰጠ መሆኑን ጠቅሰው፣ ባለፈው ወር መጨረሻ ሀገር አቀፍ ዘመቻ በማካሄድ ለ1866 ሕፃናት የኩፍኝ ክትባት፣ ለ2103 ሕፃናት ቫይታሚን ኤ፣ ለ2095 ሕፃናት ደግሞ የኑትሪሽን አገልግሎት መስጠታቸውን አስታውቀዋል፡፡ አሁን በጣቢያው ያለው ሁኔታ አስቸኳይ ጊዜ ስላልሆነ፣ የክትትል ሥራ እያከናወኑ ነው፡፡ በዚሁ መሠረት ከጋራ መፀዳጃ ወደ ቤተሰብ መፀዳጃ ግንባታ እየገቡ ነው፡፡ በጤና ጣቢያ፣ በት/ቤት፣ በመኖሪያ አካባቢ፣ በቡና ጠጡ ፕሮግራም የጤና ትምህርት ይሰጣሉ፡፡

ከአምስት ዓመት በታች አንድ፣ ከአምስት ዓመት በላይ ሁለት በአጠቃላይ ሦስት የተመላላሽ ሕክምና ይሰጣል፡፡ ከየዞኑ በጠና የታመሙ በሽተኞች ወደ ጣቢያው ሲመጡ ተገቢውን ሕክምና ይሰጣሉ፤ ከአቅም በላይ ከሆነ ለአሶሳ ሆስፒታልና ከባሰም እስከ አዲስ አበባ ድረስ ሪፈራል ይልካሉ፡፡ በጣቢያው የላይኛው የመተንፈሻ አካል፣ የቆዳና የዓይን በሽታ ጐልቶ ይታያል፡፡ ውሃማ ተቅማጥ ደግሞ ለሦስት ወራት ሕፃናትን አጥቅቶ ነበር፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ከዓለም ምግብ ፕሮግራም ጋር ተቀናጅተው ባደረጉት ጥናት፣ ለስደተኞቹ የሚቀርበው ውሃ ንፁህ ቢሆንም በአጠቃቀም ደረጃ ስለሚበከል መሆኑን ደርሰውበታል፡፡ በጁን ወር የመጀመሪያ ሳምንት ደግሞ የወባ በሽተኞች ቁጥር ጨምሯል፡፡ ኅብረተሰቡ አጐበር እንዲጠቀም፣ ያቆረ ውሃ እንዲያፋስስ ሰፊ ቅስቀሳ እያካሄዱ መሆኑን ዶክተሩ ገልጸዋል፡፡ ለማንኛዋም ወላድ አጐበር ከመሰጠቱም በላይ ለሁሉም ለማዳረስ ተጨማሪ አጐበር ጠይቀዋል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ከ70 ሰዎች 41 የወባ በሽተኛ መገኘታቸው ስጋት በመፍጠሩ ነው፡፡

የወባ ወረርሽኝ ቢከሰት ግን የመላከል አቅም እንዳላቸው ዶክተር ሙሉጌታ ተናግረዋል፡፡ በመጠለያ ጣቢያ ያለው ት/ቤት ዘንድሮ ነው የተከፈተው፡፡ ከ1ኛ እስከ 4ኛ ክፍል የሚያስተምር ሲሆን በአጠቃላይ 2028 ተማሪዎች፣ 18 ስደተኛና አራት መደበኛ መምህራን አሉት፡ የመምህራኑ ቁጥር አነስተኛ በመሆኑ አንድ መምህር ለ107 ተማሪዎች ያህል እንደሆነ የገለፀው የት/ቤቱ መምህር አቶ ጥላሁን ጓዴ ነው፡፡ አሁን የሚያስተምሩት በቆርቆሮ ዳስ ውስጥ ነው፡፡ የአዲስ ት/ቤት ግንባታ እየተፋጠነ በመሆኑ በመጪው ዓመት ወደ አዲሱ ት/ቤት እንደሚገቡ የጠቆመው መምህሩ፤ ባለፈው ሳምንት በጣቢያው በተከሰተ አውሎንፋስ አንድ ተማሪ ቆርቆሮ መትቶት እንደሞተ ተናግረዋል፡፡ ሆኖም ከግማሽ ቀን በላይ በመማር ማስተማሩ ሂደት ላይ የጐላ ተፅዕኖ እንዳልተፈጠረ አቶ ጥላሁን ገልጿል፡፡ ታላታ በበክር የ14 ዓመት ታዳጊ ናት፡፡ ታላታ አገሯ እያለች የትምህርት ዕድል ስላላገኘች በባምባሲ መጠለያ ጣቢያ የ1ኛ ክፍል ተማሪ ናት፡፡ ወደ ባምባሲ የስደተኞች ጣቢያ የመጣችው ከአራት ቤተሰቦቿ ጋር ነው፡፡ ዐረብኛ፣ እንግሊዝኛና ሂሳብ እንደሚማሩና መምህራኑ ጥሩ ስለሆኑ የእውቀት ጭላንጭል እያየች ስለሆነ በፍቅር እየተከታተለች መሆኗን ገልፃለች፡፡ ሰላም ሰፍኖ ወደ አገሯ ስትመለስ እሷም መምህር ሆና ያልተማሩ ወገኖቿን የእውቀት ጥማት እንደምታረካ አስረድታለች፡፡

ቤተልሔም ጥላሁን የሳይኮሶሻል ሄልዝ ፊልድ ኦፊሰር ናት፡፡ 15 ስደተኛ ሴቶች ለአምስት ወር በሙያ (በስፌትና በጥልፍ) ሥልጠና ተከታትለዋል፡፡ ሥልጠና የሚሰጠው ገቢያቸውን እንዲያሳድጉ ብቻ ሳይሆን፣ ያሉበት ስፍራ ለሴቶች ምቹ እንዲሆን፣ ሴቶች ተዋውቀውና ተቀራርበው እየተወያዩ ማኅበራዊ ግንኙነታቸውን እንዲያጐለብቱ፣ … ለማድረግ እንደሆነ ቤተልሔም ተናግራለች፡፡ ካሁን በፊት 150 ሴቶችና 60 ወንዶች በምግብ ዝግጅት፣ 30 ሴቶች ደግሞ በኪሮሽ ሥራ ማሠልጠናቸውን ገልጻ፣ ሠልጣኞቹም ምርቶቻቸውን ሸጠው ገቢ ማግኘታቸውን ተናግራለች፡፡ ወጣቶች ዝም ብለው ሲቀመጡ ለአዕምሯቸው ጤንነት መጥፎ ስለሆነ፣ ራሳቸውን እንዲያዝናኑ የተለያየ ስፖርታዊ ሥልጠናና ለስደተኞቹ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት የተለያየ የአቅም ግንባታ መስጠታቸውን፣ ለሴቶች የማኅበረሰብ ውይይት፣ ወጣቶች በሱስ እንዳይጠመዱ፣ የተለያዩ ሥልጠናዎች መስጠታቸውን፣ እንዲሁም የአካባቢያቸውን ባህል እንዳይረሱና ዘና እንዲሉ፣ ባህላዊ አከባበር ማድረጋቸውን ተናግራለች፡፡ የ30 ዓመቷ ማይዳ ኢብራሂም የጊዘን አካባቢ ነዋሪ ናት፡፡ ወደ ባምባሲ የስደተኞች ጣቢያ የመጣችው ስድስት ልጆቿንና አሮጊት አያቷን በአጠቃላይ ስምንት ቤተሰብ ይዛ ነው፡፡

የምትኖርበት አካባቢ በድንገት በአውሮፕላን ቦንብ ሲመታ፣ የተወሰኑ ልጆቿን ይዛ ነው ነፍሴ አውጪኝ ያለችው፡፡ ድብደባው ጋብ ሲል ነው የተቀሩትን ልጆች ተመልሳ የወሰደቻቸው፡፡ ነገሩ ቀዝቀዝ ሲል ደግሞ ተመልሳ በጣም ጠቃሚ ናቸው ያለቻቸውን ዕቃዎች ወስዳ ሸሸች፡፡ ማይዳ ከባሏ ጋር የተለያየችው በጦርነቱ ነው፡፡ ይሙት ይኑር የምታውቀው ነገር የለም፡፡ ከባለቤቷ ወይም ከሚስቱ ወይም ከወላጆቻቸው የተለያዩ ልጆች በማለት በየጊዜው እየመጡ ቢመዘግቧቸውም ማንኛውም ስደተኛ ከሚያገኘው መደበኛ ራሽን በስተቀር ምንም አላገኘችም፡፡ እንደ አንዳንድ ሴቶች መሠልጠን ብትፈልግም ዕድሉን እንዳላገኘች ትናገራለች፡፡ አቶ ሀሰን አቡና ካሪም የ49 ዓመት ጐልማሳ ናቸው፡፡ የሚኖሩበት የሻንከሩ አካባቢ በአውሮፕላን ሲደበደብ ሁሉም ነፍሱን ለማትረፍ በየአቅጣጫው መበታተኑን ይናገራሉ፡፡ እሳቸውም ሰባት ቤተሰባቸውን ይዘው ነው የተሰደዱት፡፡

ከቤት ንብረታቸው መፈናቀል ሳያንሳቸው በስደትም ጥሩ ዕድል አላጋጠማቸውም፡፡ ባምባሲ መጠለያ ጣቢያ ከደረሱ በኋላ የጀርባ ሕመምተኛ ሆኑ፡፡ በየጊዜው ወደ ጤና ጣቢያው ቢሄዱም ምንም እንዳልተሻላቸው ገልጸዋል፡፡ ስደተኛው በየጎጆው ፊት-ለፊት የተከለው ዛፍ ፀድቆ የአንድ ዓመት ዕድሜ አስቆጥሯል፡፡ ስደተኞቹ ማገዶ ፍለጋ የአካባቢውን ደን እንዳይጨፈጭፉ ምድጃና ነጭ ጋዝ ይቀርብላቸዋል፡፡ በአጠቃላይ የስደተኛ ስሜት እንዳያድርባቸው በተቻለ መጠን ጥረት እየተደረገ ነው፡፡ ሐሙስ ዕለት በባምባሲ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ የገበያ ቀን ነው፡፡ በገበያው መኻል በሁለት ቦታ ዲናሞ እየተንደቀደቀ የተለያዩ ሞባይሎች ቻርጅ ይደረጋሉ፡፡ አሮጌ ልብሶች የሚጠግኑም አሉ፡፡ ብስኩት፣ ዳቦ፣ አምባሻ፣ ሥጋ፣ ቲማቲም፣ ሙዝ፣ ሎሚ፣ የማገዶ እንጨት፣ ስንዴ፣ ምስር፣ ዘይት፣ ሽርኩርት፣ የተለያዩ ሸቀጣ ሸቀጦች፣ ጨጨስ የሚባል የገንፎ ማባያ ቅጠልና ተከትፎ ሥጋ ላይ የሚጨመር ኮድራ የተባለ ቅጠል፣ … ብቻ ሁሉም ያለውን ይዞ ወጥቶ ሸማች ይጠባበቃል፡፡

Published in ባህል

            የእግር ኳስ ፌዴሬሽን ቅሌት የክፍለ ዘመኑን ሪከርድ ሰብሯል!

“ስህተት የፈፀምነው ስለሰራን እኮ ነው” (አንድ እየሰሩ ሺውን መናድ?)

                    የኢትዮጵያ የእግር ኳስ ፌዴሬሽን ተወዳዳሪ የሌለው ቅሌት በመፈፀም የዓመቱን ሳይሆን የክፍለ ዘመኑን ሪከርድ መስበሩን በሳምንቱ መግቢያ ላይ አብስሮናል!! (Scandal of the Century ይሏል ይሄ ነው!) እኔና እንደኔ ያሉ አንዳንድ ገራገሮች ነገርዬውን በቅሌት ብቻ ብናልፈውም ጥቂት የማይባሉ ደመ - መራራ የአገሬ ልጆች ግን የፌዴሬሽኑን እሳት አደጋ የማይመልሰው ከባድ አገራዊ ጥፋት “ከአገር ክህደት ለይተን አናየውም” የሚል መግለጫ እንዳወጡበት ሰምቻለሁ (ደማቸው ፈልቶ እኮ ነው!) ደግነቱ ግን መግለጫው አደባባይ አልወጣም፡፡ በየልባቸው ውስጥ ቀርቷል ተብሏል፡፡ ባለፈው እሁድ የብሄራዊ ቡድናችንን ድል ተከትሎ የተፈጠረውን ደስታ ሽፋን አድርገው፣ የሰው ንብረት ሲሰባብሩ ነበር የተባሉ አንዳንድ ጋጠወጦች ደግሞ ምን አሉ መሰላችሁ? “የፌዴሬሽኑ አመራር የፈፀመው ስህተት ከአሸባሪነት አይተናነስም!” ብለው ቁጭ አሉ፡፡

ለእነዚህ እንኳ ጆሮም ልንሰጣቸው አይገባም ባይ ነኝ። መቼ ራሳቸው ደግና ክፉውን ለዩና ነው ፍርድ የሚሰጡት፡፡ በአገር የደስታ ቀን ደስታ የሚያጠፉ ዋልጌዎች እኮ ናቸው! እነዚህንስ ለቃቅሞ ማረምያ ቤት መወርወር ነበር - ከጋጠወጥነታቸው ታርመው እንዲወጡ፡፡ ወደ ፌዴሬሽኑ ጉዳይ ስንመለስ--- እኔን ምን እንዳስገረመኝ ታውቃላችሁ? የፌዴሬሽኑ አመራሮች በእነሱ ብሶ በእኛ ላይ መነጫነጫቸው! ቆይ ግን ---አገርን ያህል ነገር ንደው፣ በስንት መከራ የተገነባውን አፍርሰው “ተሳስተናል” ስላሉ ብቻ በሰላም ወደየቤታችሁ ግቡ እንዲባሉ ፈልገው ነበር እንዴ ? ( “ደፍረውናል” ያለው ማን ነበር!) እናላችሁ-----አመራሮቹ መግለጫ የሰጡ እለት ከጋዜጠኞች ያልተጠበቁ ጥያቄዎች ሲወረወርባቸው የሚናገሩት ሁሉ ጠፍቷቸው ሲዘባርቁ ነበር አሉ፡፡ መዘባረቁን ያመጣው ምን መሰላችሁ --- “አመራሩ ሃላፊነቱን ይለቃል ወይ?” የሚለው የጋዜጠኞች ዱብእዳ ጥያቄ ነው፡፡ በቃ--- የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችን መልስ እኮ ነው የሰጡት፡፡ (እግር ኳስ ፖለቲካ ነው የሚባለው ለካ እውነት ነው!) በተለይ የፌዴሬሽኑ ዋናው ፕሬዚዳንት እኮ በትርፍ ሰዓታቸው በፓርቲ መሪነት የሚሰሩ ነው የመሰሉት። (ንግግራቸው ቁጭ እኮ ነው!) የለም ተሳስተሃል ከተባልኩ ደግሞ የፓርቲ መሪዎች የሚሰጡትን ዓይነት መልስ ሸምድደው እንደመጡ በእርግጠኝነት እገምታለሁ፡፡

እኔን ካላመናችሁኝ ደግሞ ራሳቸው ፕሬዚዳንቱ ከተናገሩት ልጥቀስላችሁ ---- “መጀመርያ ይሄን ነገር እንደሰማሁ ሥልጣኑን እለቃለሁ ነበር ያልኩት” ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣በኋላ ግን ሃሳባቸውን እንደቀየሩ ገልፀዋል (ሰይጣን አሳስቷቸው ይሆን?) የፌዴሬሽኑ ሃላፊ ከሥራ የመልቀቅ ሃሳባቸውን የቀየሩበትን ምክንያት ስትሰሙ ነው እኔ ካልኩት ሃሳብ ጋር (የፖለቲካ መሪነት ከምትለዋ ማለቴ ነው) በደንብ የምትስማሙት። ምን አሉ መሰላችሁ --- “ለማን ጥለን እንሄዳለን? ---የሚቀጥል ይኖራል የማይቀጥልም --- ክለቦች ከፈለጉን፣ ጉባኤው ከፈለገን ---መንግስት ከፈለገን -- የምንቀጥልም የማንቀጥልም እንኖራለን --- የናንተ ጭንቀት አይደለም --- ጉባኤው ይወስነዋል” የሚል ምላሽ ሰጡ - ለተሰበሰቡት የስፖርት ጋዜጠኞች። እውነቴን እኮ ነው የምላችሁ ---- አምባገነን የሥልጣን ጥመኞች ከሥልጣን የመልቀቅ ጉዳይ ድንገት ሲነሳባቸው የሚሰጡትን መልስ እኮ ነው ቃል በቃል ቁጭ ያደረጉት (እኔማ “አወይ መመሳሰል” አልኩኝ!) ሁሉንም አመራሮች ምን ያመሳስላቸዋል ያላችሁኝ እንደሆነ --- የራሳቸውን ጥፋት ወደማይናገረውና የማይጋገረው ግኡዙ ፌዴሬሽን ለማስተላለፍ ያልፈነቀሉት ድንጋይ አለመኖሩ ነው እላችኋለሁ፡፡

እዚያው መግለጫ በሰጡበት መድረክ ያጉተመተሙት ነገር ቃል በቃል ባይሆን እንኳን በደምሳሳው - “ እርግማን እንጂ ምስጋና የሌለበት ፌዴሬሽን---ይብላኝ ለሚተካው እንጂ እኛማ በቅቶናል-- ዝርክርክ ፌዴሬሽን ነው” ወዘተ---በማለት ከመቅፅበት ባይተዋርና ባዳ አድርገውታል - የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑን (ዋት ኤ ፒቲ! አለ ፈረንጅ) በነገራችሁ ላይ የጥፋቱ አንዱ ተጠያቂ ሆነው የቀረቡት የፌዴሬሽኑ አመራር ያቀረቡት ሰበብ ጭንቅላት አሲዞ “ወይ እቺ አገር!” የሚያስብል ነው፡፡ ምን ቢሉ ጥሩ ነው --- ሌላ የግል ሥራ እንዳለባቸውና በቂ ጊዜ እንደሌላቸው በግልፅ ተናግረዋል (አድናቂያቸው ነኝ !) እኔ የምለው ግን --- በቂ ጊዜ ያለው ሰው ለፌዴሬሽኑ ጠፍቶ ነው ወይስ ሥራው በበጎ ፈቃደኝነት ነው የሚሰራው? (ያለገንዘብ ማለቴ ነው!) የኢትዮጵያ የእግር ኳስ ፌዴሬሽን አመራሮች በይቅርታ ብቻ እንታለፋለን ብለው ያሰቡት በአንድ ምክንያት ሳይሆን አይቀርም ብዬ አስባለሁ።

ጥፋታችንን በአደባባይ ካመንን ህዝቡን አስደምመነው ሁሉም ነገር “ቢዝነስ አስ ዩዥዋል!” ይሆናል በሚል ሳይሆን እንደማይቀር በግምት ላይ የተመሰረተ ጥርጣሬ አለኝ፡፡ እንዴት መሰላችሁ ---- ስህተትን ማመን ለእኛ ብርቃችን መስሏቸው እኮ ነው! ይሄ ሁሉ የመጣው ደግሞ ለመረጃ ዋጋ ስለማይሰጡ በተፈጠረ የመረጃ ክፍተት ይመስለኛል! ለመረጃ ዋጋ ቢሰጡማ--- ድልን ወደ ሽንፈት ሊለውጥ አቅም ያለው የብጫ ካርድ መረጃ የት እንደገባ አናውቅም በማለት፣ ስንገነባ የከረምነውን የኳስ ውጤት አይንዱብንም ነበር፡፡ እናም በዚህ አጋጣሚ “ስህተት ሰርተናል” ብሎ በአደባባይ ማመን ብርቃችን እንዳልሆነ የሚመለከተው ወገን ሁሉ እንዲያውቅልን እንፈልጋለን፡፡ እድሜ ለኢህአዴግ! ላለፉት 22 ዓመታት እኮ ይሄንኑ ነው ያስተማረን - ሁሌም መሳሳት! ሁሌም ስህተትን ማመን! (ሂስን መዋጥ ይሉታል በፓርቲው ቋንቋ!) ለነገሩ ስህተትን በማመንና አጥፍተናል ብሎ በይፋ በመናገር አውራው ፓርቲያችን ፈርቀዳጅ ባይሆን ኖሮ፣ የእግር ኳስ ፌዴሬሽናችን በአንድ ጊዜ ሁለት ሪከርዶችን ይሰብር ነበር - አንደኛው የክፍለዘመኑ ቅሌት በሚለው ዘርፍ ሲሆን ሌላው ተሳስተናል በሚለው ዘርፍ ይሆን ነበር፡፡ ችግሩ ግን ተቀደመ፡፡

እኔ ግን የፌዴሬሽኑን አመራሮች በተመለከተ አሁንም ድረስ ያልተዋጠልኝ ነገር ምን መሰላችሁ? እግር ኳስ ተጫውታችሁ ዋንጫ አምጡ ያላቸው እኮ የለም! ምነው ታዲያ አንድ ተጫዋች ያየውንና በፊፋ የተላከውን ብጫ ካርድን የተመለከተ መረጃ ለሚመለከተው ወገን ማቀበል እንዲህ አቀበት ሆነባቸው? ሌላው የገረመኝ ጥፋትን ከማመን ጎን ለጎን የተደረደሩት ሰበቦች ናቸው - “በሌሎች ጉዳዮች ተወጥረን ነበር”፣ “የተጫዋቾችን ቪዛ ለማስመታት ስንሯሯጥ ነበር” ወዘተ--- ፋይዳቸው ፈፅሞ ሊገባኝ አልቻለም፡፡ እንዴ --- ዋና ስራቸው ምን ሆነና? ለምሳሌ--- አንድ የፖለቲካ ፓርቲ የምርጫ እለት እጩዎች አልመለመልኩም ቢል የሚሰማው ያገኛል እንዴ? (እንስራዋን ጥላ ወንዝ ወረደች አሉ!) አንድ የስፖርት ጋዜጠኛ ሹክ ያለኝ ነገር ደግሞ ትንሽ አስደንግጦኛል፡፡ በአመራሮቹ መካከል መኮራረፍ… አለመከባበር… የቀናነት ጉድለት…በአጠቃላይ ኮሚዩኒኬሽን የሚባል ነገር ጨርሶ እንደሌለ ነግሮኝ የባሰ ተስፋ አስቆርጦኛል። ነገርየው ለጊዜው ያስደንግጠኝ እንጂ ረጋ ብዬ ሳስበው እንደ እግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት ሃሳቤን ቀይሬአለሁ፣ ለካስ --- የኩርፊያ ነገር የጦቢያችን ልዩ ምልክት ነው፡፡

አሁን ለምሳሌ ከጥቂት አመታት በፊት እንደ ፖለቲካ ፓርቲ ለሁለት የተሰነጠቀው የኢትዮጵያ ሴት ደራሲያን ማህበር አመራሮች እርስ በርሳቸው ይነጋገራሉ ብላችሁ ታስባላችሁ? (የሚያስታጥቃቸው አጥተው ነው እንጂ ከመጨራረስ ወደኋላ የሚሉ አይመስለኝም) ስንቶቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ናቸው ከኢዴፓ ጋር መልካም ግንኙነት ያላቸው? (ያልተኮራረፉት ማለቴ ነው!) ኢህአዴግና መድረክ አንነጋገርም ብለው ከተፈጠሙ ስንት ዘመናቸው ሆናቸው? ፖለቲከኞችስ እሺ---የሚፎካከሩበት ጉዳይ ራሱ እሳት ነው (የስልጣን የቤት ስሙ እኮ እሳት ነው!) ግን እሱም ቢሆን አደጋ አለው(ሥልጣን ያለስልጣኔ “hard” ነዋ!) ቆይ ቴሌና መብራት ሃይል---ውሃ ፍሳሽና መንገድ ትራንስፖርት መች በወጉ ይነጋገራሉ? ከቶውንስ መች ይናበባሉ? ቢነጋገሩ ኖሮማ---ከተማዋ በየተራ እየተቆፋፈረች ይሄን ሁሉ ምስቅልቅል አናይም ነበር (ማን ነበር ምስቅልቅሉ ቢኖርም የእድገት ምስቅልቅል ነው ያለው?) እናላችሁ… ነገርዬው አገራዊ ጉዳይ (ችግር) በመሆኑ አገራዊ መፍትሄ ሊበጅለት ይገባል እላለሁ።

በህግና በቁጥጥር ወይም በተጠያቂነት ምናምን ግን አይደለም (እንደማያዋጣ አይተነዋላ!) ይኸውላችሁ --- ይሄ ችግር የሚፈታው በሌላ ሳይሆን በአገር ሽማግሌ ብቻ ነው!! ቀልድ እንዳይመስላችሁ --- ነገርየው ትንሽ መረር፣ ትንሽ አረር ብሏል፡፡ እስቲ አስቡት----ግብፆች በአባይ ግድብ ጉዳይ ላይ ገዢው ፓርቲ ወይም ተቃዋሚ ሳይሉ በአንድ ሸንጎ ተሰይመው ሲያሴሩብን ኢህአዴግና ተቃዋሚዎች “የአገር ጉዳይ ነው”ብለው ለአምስት ደቂቃ እንኳን መች አንድ ላይ ተቀመጡ (እርግማን አለብን ይሆን?) የሆኖ ሆኖ ግን ይሄ አገርን እስርስር ያደረገ የኩርፊያ ሰንሰለት የግድ መበጠስ አለበት ባይ ነኝ ! በነገራችሁ ላይ የሽማግሌዎች ቡድን የሚያስፈልገው የተቃዋሚ አመራሮች ወህኒ ቤት ሲገቡ ለማስፈታት ብቻ እኮ አይደለም፡፡ እንዲህ ራሳችንን በኩርፊያ ስናስርም ሽምግልና ያስፈልገናል - ከራሳችንም ከሌላውም ጋር የሚያስታርቀን፡፡ ያለበለዚያ እንደ ኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ብዙ የቅሌት ሪከርዶችን ስንሰብር መክረማችን ነው፡፡ (መናናቅ ባመጣው ጦስ!) የፖለቲካ ወጌን ላጠናቅቅ ስል አንድ ሸጋ ወሬ ደረሰኝ (መረጃም ማስረጃም የሌለው) ምን መሰላችሁ---ከፌዴሬሽኑ አመራሮች መካከል ሁለቱ ሂሳቸውን የዋጡ አመራሮች የሥራ መልቀቂያ ጠየቁ የሚል ነው። አንጀቴ ቅቤ ጠጣ የሚያስብል ባይሆንም አበረታች እርምጃ መሆኑን ግን ማንም አይክደውም። አገር እየናዱ ይቅርታ ከመጠየቅ የሥራ መልቀቂያ መጠየቅ ይሻላል ባይ ነኝ (ተጠያቂነቱም ሳይቀር ነው ታዲያ!)

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

                  እኔ የምለው…ለቤት ምዝገባው ተብሎ የፈረሱ ትዳሮች አሉ የሚባለው ነገር…የምር እውነት ነው እንዴ? አሀ… ግራ ገባና! እውነት ከሆነ እኮ…አለ አይደል…የትዳርና የአዳር ልዩነት ሊጠፋ ነው ማለት ነው! ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ባልና ሚስት ለሽ ብለው ተኝተዋል፡፡ ሚስት ሆዬ ለካ የሆነ ህልም አይታ ኖሮ ብድግ ብላ ማልቀስ ትጀምራለች፡፡ ባልም ደንግጦ ይነቃል፡፡ “ምን ሆንሽ፣ በውድቅት ሌሊት እንዲህ የሚያስለቅስሽ ምንድነው?” ይላታል፡፡ እሷም…“አንድ መልከ መልካምና ሀብታም ሰውዬ ከአንተ ነጥቆ ሲወስደኝ አየሁ…” ትለዋለች፡፡ ባልም እያጽናናት... “የእኔ አበባ፣ በቃ አታልቅሺ፡፡ ህልም እኮ ነው” ይላታል፡፡ እሷ ሆዬ ምን ብትል ጥሩ ነው…“ታዲያ የሚያስለቅስኝ ህልም መሆኑ አይደል!” ልጄ… ልብ ያለው ልብ ቢል አሪፍ ነው፡፡ አሀ…ባሏ 10/90 የተመዘገበው ሚስት “40/60 የተመዘገበ ከአንተ ነጥሎ ሲወስደኝ በህልሜ አየሁ…” ልትል ትችላለቻ! ነገርዬው…አለ አይደል… “ለድካም የጣፈኝ ብነግድ አይተርፈኝ” ነው፡፡ ነገራችን ሁሉ ‘ህልም’ ሆኖ እየቀረ አስቸጋሪ ሆኗል፡፡

እና ገና “ሁለታችን ለየብቻችን ተመዝግበን ሁለት ቤት እናገኛለን…” በሚል ትዳር የሚፈርስበት ዘመን ከተደረሰ የምር ያሳስባል፡፡ እኔ የምለው…ይሄ ቢግ ብራዘር ምናምን የሚሉት ነገር ላይ ልጅቷ “እነሆ በረከት…” ተባብላ ትንሽ አንዳንዶችን ደማቸውን ከፍ፣ ስኳራቸውን ዝቅ አደረገችው አይደል! እኔ ግራ የሚገባኝ ምን መሰላችሁ…ልጅቱ ሠራችው የተባለው በምንም መለኪያ ‘ብራቮ’ የሚያሰኝ አይደለም፡፡ መጀመሪያ ላይ በኤፍ.ኤሞች ላይ “ቮት አድርጉላት” ስንባል የነበረው ግራ ይገባኛል፡፡ መጀመሪያ ‘ቢግ ብራዘር’ የሚባለውን ነገር የሚከታተለው ህዝባችን አንድ በመቶስ ይሞላል? በማያውቀው ነገር፣ ወክሎ ላልከው ሰው ድምጽ ስጥ ተብሎ ‘ሎቢ’ የሚካሄድበት ለምን እንደሆነ ግራ ይገባኛል! ብዙዎች ተበሳጭተው አስተማሪዋ ላይ ያንን ሁሉ ያወረዱባት እኮ ከመሬት ተነስተው ላይሆን ይችላል፡፡ ድምጽ ሰጡ፣ ድምጻቸው ግን ያላሰቡትን አመጣባቸው፡፡ ‘ፎርቹን’ ጋዜጣ ላይ አንድ ቋሚ ጸሀፊ “እንደ ማህበረሰብ፣ ለገንዘብና ለዝና ሲሉ ምንም ወደሚያደርጉ ህዝቦች ዝቅ ብለናል…” ብሎ ያሰፈረው የእውነትም የዘንድሮ አከራረማችንን የሚገልጽ ይመስለኛል፡፡ ትዳር አፍረስው እያንዳንዳቸው በየራሳቸው ቤት ለማግኘት የሚሞክሩ ካሉ ዞሮ፣ ዞሮ ጥቅም (‘ገንዘብ’) ፍለጋ ነው፡፡

እነሱ ትዳራቸውን ‘በጊዜያዊነት’ አፍርሰው ‘ሁለት ቤት’ ሲፈልጉ የሌሎችን አንድ ቤት እንኳን የማግኘት ዕድል እያበላሹ እንደሆነ ዘወር ብለው አለማየታቸው ያሳዝናል፡፡ እግረ መንገዴን ይቺን ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…የባልና የሚስት ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ስሙኝማ፡፡ ባል ሆዬ ቤተክርስትያን ስብከት ሲሰማ ውሎ ይመጣል። ቤት እንደ ደረሰ ወዲያውኑ ምን ቢያደርግ ጥሩ ነው… ሚስቱን ብድግ አድርጎ ይሸከማትና ቤቱን መዞር ይጀምራል፡፡ ሚስትም ነገርዬው ያልተለመደ ይሆንባትና… “ቄሱ ሚስቶቻችሁን ተሸክማችሁ ፍቅራችሁን አሳዩ አሉ እንዴ?” ብላ ትጠይቃለች፡፡ ባልም ምን ብሎ መለሰ መሰላችሁ…“የራሳችሁን ሸክም ራሳችሁ ቻሉ ነው ያሉን…” ብሏት አረፈው፡፡ እኔ የምለው…ይሄ ሁሉ ባል ጂም ቁና፣ ቁና ሲተነፍስ የሚያመሸው ለካ ቤት ሲገባ ሸክም ስለሚጠብቀው ነው! ቂ…ቂ…ቂ… ስሙኝማ…ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ይሄ የኳሳችን ነገር…እንዲሁ “አሁንስ መልክ ያዘ…” ስንል ‘በግልባጩ’ እየሄደ አስቸገረን፡፡ ይሄ በተጫዋች ተገቢነት የተፈጠረው ነገር ለእኔ በምንም መለኪያ “የፈሰሰ ውሀ…” የሚባል አይመስለኝም፡፡ ‘ውሀ እንዳይፈስ’ ማድረግ ካልተቻለ እኮ…አስቸጋሪ ነው፡፡

ስሙኝማ… ካነሳነው አይቀር…ከበቀደሙ ጨዋታ ጋር በተያያዘ…አለ አይደል፣ ቆም ብለን ልናስባቸው የሚገቡ ነገሮች ያሉ አይመስሏችሁም? የምር እኮ… ገና ለገና የአባይ ጉዳይ የጦፈበት ጊዜ ነው ተብሎ… ዳኞቹ ግብጻውያን መሆናቸው ያንን ሁሉ የአየር ሰዓት ይዞ ‘ዓቢይ ጉዳይ’ መሆኑ ግራ ያጋባል፡፡ ምን መሰላችሁ…ይሄ የ‘ኮንስፒሬሲ ቲዮሪ’ ነገራችን…አለ አይደል… ሁሉም ነገር ላይ “ምን ተንኮል ቢያስቡብን ነው?” እያስባለን ጠላት ፈላጊ አድርጎናል፡፡ ዳኞቹ የሚመጡት ከግብጽም ሆነ ከፊጂ የሚያጫውቱባቸው ህጎች እነዛው ናቸው፡፡ እኛ የምንዳኛቸው በዘር ግንዳቸው ሳይሆን በእግር ኳስ ህጎቹ አተረጓጎማቸው መሆን አለበት፡፡ አንዳንድ ሜዲያ ላይ ግን ከዳኝነት ብቃታቸው ይልቅ ዜግነታቸው ‘ሰበር ዜና’ ነገር እየሆነ ብዙዎች ጨዋታውን ከጅምሩ በጥርጣሬ እንዲያዩ አድርጓቸዋል፡፡ (እግረ መንገድም…በስፖርት ፕሮግራሞችም ሆነ በሌሎች ጉዳዮች የአሌክትሮኒክስ ሜዲያው ራሱን በጥንቃቄ ማየት ያለበት ጊዜ አሁን ይመስለናል፡፡ አንዳንድ ‘እያመለጡ’ ያሉ ነገሮች የምር አሳሳቢ ናቸው፡፡

በነገራችን ላይ በስፖርት ሚዲያው አሪፍ እየሠሩ ያሉ እንዳሉ መጥቀስም አሪፍ ነው…ከእነጥቃቅን ስህተቶቻቸው፡፡) እናላችሁ…የኳሳችንን ነገር በተመለከተ ሚዲያ ውስጥ ያለን ሰዎች ከ‘እኛ ውጪ’ ያለውን ዓለም ብቻ ሳይሆን ‘የራሳችንን ዓለም’ ማየት ያለብን ይመስለኛል፡፡ አንደኛ ነገር መልካም መመኘት እንዳለ ሆኖ ህዝቡ… “ወይ ማሸነፍ ወይ ሞት!” አይነት ስሜት እንዲያድርበት የሚያደርጉ አቀራረቦች አሪፍ አይደሉም፡፡ ደግሞላችሁ…ከጨዋታው በኋላ ታየ የተባለው የ‘ደስታ ስሜት’ አንዳንድ ነገሮች እንዴት መልካቸውን እየለወጡ እንደሆነ ደስ የማይል ምልክት ነው፡፡ ዋናውን እውነተኛ ደስታ በተጓዳኝ የታዩ ጥፋቶች ነገሮች ላይ ጥላ እያጠሉባቸው ነው፡፡ እዚቹ ከተማችን ውስጥ በርካታ ቦታዎች ላይ የታዩ አላስፈላጊ ምግባሮች የምር ሊያሳስቡን ይገባል፡፡ ሰው የለፋበት ንብረቱ ለምን ይወድማል? ሰዎችስ ደስ ሊላቸው በሚገባ ሰዓት ለምን ለራሳቸው ደህንነትና ለንብረታቸው እንዲሰጉ ይሆናል? ሰዎች ተጎድተዋል፣ ንብረቶች ወድመዋል፡፡ “ለምን?” ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ አንድ ወዳጄ የአንድ ትልቅ ሆቴል በር ላይ የነበሩ የጥድ ዛፎች እየተነቀሉ መወሰዳቸውን ሲነግረኝ ነበር፡፡ ለምን? በጣም ልቅ የሆኑ ነገሮች እየበዙ ነው፡፡

በደስታ ስም ሰዎች መኪናቸው የሚሰበር ከሆነ፣ የማህበራዊ አገልገሎት መስጫዎች የሚወድሙ ከሆነ፣ ሰዎች ጉዳት የሚደርስባቸው ከሆነ… ምናልባት ወደፊት ደስታችንን በተወሰነ ክልል እንድንወስን የምንገደድበት ጊዜ ሊመጣ ይችላል፡፡ ሰዋችን ‘ደመ መራራ’ ሆኗል፡፡ በትንሽ ነገር ሆድ ይብሰዋል፣ ይቆጣል…ዓለም ሁሉ በእሱ ላይ የሚያሴር ይመስለዋል፡፡ እንደዚህ አይነት ስሜቶች እንዲገነቡ በማድረግ የሚዲያው ሚና አለ፡፡ በቢጫና ቀይ ካርድም ይሁን በሌላ ምክንያት ያልተገባ ተጫዋች ማሰለፍ ቅጣት ያስከትላል፡፡ አለቀ፡፡ የፊፋ የኳስ ህጎች የማናውቅ ሰዎች እንኳን ይህን በ‘ተራ ሎጂክ’ ልናውቀው የምንችለው ነው፡፡ ጥፋት ይነስም ይብዛም…ዋጋ ያስከፍላል፡፡ የፊፋ መግለጫ ሲወጣ ወዲያውኑ ለህዝቡ መግለጽ ያለብን የሚዲያ ሰዎች ነን፡፡ የኳስ ህጎችን የማናውቅ የስፖርት ጋዜጠኞች አለን ለማለት ያስቸግረኛል፡፡ ሁኔታውን ወዲያውኑ ለህዝቡ ማስረዳት ያለብን እኛ ነን፡፡ የሚያሳዝነው ነገር ምን መሰላችሁ…አንዳንድ አቀራረባችን “ፊፋ እኛን ጥሎ ደቡብ አፍሪካን ለማሳለፍ ፈልጎ ነው…” አይነት ስሜት የሚያሳድሩ ነበሩ፡፡

እና የኳስ ተመልካቾች ቢቆጡና የመጠቃት ስሜት ቢያድርባቸው በአብዛኛው ከ‘ባዶ ሜዳ’ ተነስቶ የመጣ አይደለም፡፡ ቃላቶቹ በጥንቃቄ ካልተመረጡ በስተቀር አብዛኛውን ጊዜ በቅንነት የሚቀርቡ ነገሮች እንኳን አላስፈላጊ ችግር ያስከትላሉ፡፡ ጥፋት ተሠርቷል? አዎ፣ ጥፋት ተሠርቷል፡፡ እናማ…እኛ የሚዲያ ሰዎች ይህንን ለማለት የጥፋቱ ሶርስ የሆነው ክፍልን መግለጫ የምንጠብቅበት ምክንያት ትንሽ ግራ ይገባል! ጥፋቱን ደግሞ ‘አለባብሶ ለማረስ’ ማድረጉ አለ አይደል…ትክክል አይመስለንም፡፡ ስሙኝማ…ይሄ የባልና የሚስት ‘ጊዜያዊ ሰማንያ ቀደዳ’ እውነት ከሆነ ሀሳብ አለን፡፡ የጋብቻ ሰርተፊኬት ላይ… “ይህ ስምምነት አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ሁለቱ ተጋቢዎች ለሚስማሙት ጊዜ ተቋርጦ እንደገና ሊቀጥል ይችላል” የሚል ይከተትበትማ፡፡

እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ይቺን ስሙኝማ… ባልና ሚስት በመንገድ ሲሄዱ አንድ የእኔ ቢጤ ያዩና ሚስት “ይህንን ለማኝ አልወደውም…” ትለዋለች፡፡ ባልም “ለምን? ምን አደረገሽ?” ይላታል፤ ምን አለችው መሰላችሁ…“ከትናንት ወዲያ ቤት መጥቶ ሲለምን እንጀራ በወጥ ሰጠሁት፡፡ ትናንትና ምን ይዞልኝ መጣ መሰለህ?” “ምን ይዞልሽ መጣ?” “የምግብ አሠራር ጥበብ’ የሚል መጽሐፍ፡፡” አሪፍ አይደል! እናማ…ለቤት ምዝገባ ትዳር ‘ኦን ሆልድ’ የሚሆን ከሆነ… ሰርተፊኬቱ ላይ ‘ቋሚ’… ‘ኮንትራት’… ‘ፍሪላንስ’ የሚሉ ሰንጠረዦች ይካተቱልን፡፡ ልክ እኮ ‘ለ20/80 ቤት፣ 50/50 ትዳር’ የመጣ ነው የሚመስለው! ቂ…ቂ…ቂ… ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

የአዲስ አበባ ህንፃዎች ለአሸባሪዎች ፍንዳታ የተጋለጡ ናቸው የፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ዘርፍ ፎሬንሲክ ምርመራ ዳይሮክቶሬት ፍንዳታ ዲቪዥን በስሩ ከሚያስተዳድራቸው ክፍሎች አንዱ የዛሬ አምስት ዓመት የተቋቋመው የፍንዳታ ምርመራ ዲቪዥን ክፍል ተጠቃሽ ነው። በኢንስፔክተር ታመነ ግርማ የሚመራው ይሄ ክፍል፤ ፍንዳታ ከመድረሱ በፊትና ከደረሰ በኋላ ምርመራ በማካሄድ ስለተፈፀመው ወይም ሊፈፀም ታስቦ ስለነበረው አደጋና የፍንዳታ መሣሪያ ዓይነት አስተማማኝ መረጃ ይሰጣል፡፡ በአገራችን ብዙ ጊዜ የተለመደው ፍንዳታ የእጅ ቦንብ እንደሆነ የሚናገሩት ኢንስፔክተር ታመነ፤ አልፎ አልፎ ግን በአሸባሪዎች የሚፈፀሙና ሊፈፀሙ የታሰቡ ሌሎች የፍንዳታ ዓይነቶች እንደሚገጥሟቸው ይገልፃሉ፡፡

በ19ኛው የአፍሪካ ህብረት ስብሰባ ወቅት ከኤርትራ ሰልጥነው የመጡ አሸባሪዎች አዲስ አበባን እንደባግዳድ ማድረግ የሚል ዓላማ አንግበው በተለያዩ አካባቢዎች ለማፈንዳት ያቀዱት C4 (Composition four) ወይም ልቁጥ ፈንጅ የተባለውን የፍንዳታ መሣሪያ እንደነበር ኢንስፔክተሩ ያወሳሉ። ደግነቱ ግን በህብረተሰቡ ጥቆማ አሸባሪዎቹ ጥቃቱን ከመፈፀማቸው በፊት በቁጥጥር ስር ሊውሉ ችለዋል፡፡ ይህ የፈንጂ አይነት እንደ ቅቤ የመቅለጥ ባህሪ ስላለው በማንኛውም ነገር ውስጥ በመክተት ከቦታ ቦታ ለማንቀሳቀስ እንደሚመች እና በፍተሻ ባለሙያዎች ዘንድም ጥርጣሬ እንደማይፈጥር ተናግረዋል፡፡ ፈንጂው ከሞባይል ጋር በመደወል ወይም በተሞላ ሰዓት አማካኝነት ሊፈነዳ እንደሚችል ጠቁመው ፈንጂው የተሰራው ለኮንስትራክሽንና ለመንገድ ስራዎች አገልግሎት ቢሆንም በአሸባሪዎች እጅ ሲገባ ግን ለከፍተኛ የህይወትና ንብረት ውድመት ይውላል ብለዋል - ኢንስፔክተሩ፡፡

እስካሁን በአገራችን ከተገኙ የፈንጂ አይነቶች መካከል ለመርማሪም ሆነ ለፖሊስ አስቸጋሪው ሆነው የተገኙት ቤት ውስጥ የሚሰሩና ሰው በራሱ ጥበብ የሚፈጥራቸው ፈንጂዎች ሲሆኑ እነዚህ ፈንጂዎች ከሲሊንደር ጋዝ ወይም ከድራፍት ሲሊንደር ጋር በማገናኘት እንዲፈነዱ የሚደረጉ ናቸው ያሉት ኢንስፔክተሩ ፤ በምሳሌነትም በቅርቡ በአሜሪካ የቦስተን ማራቶን ላይ የደረሰውን አደጋ ይጠቅሳሉ፡፡ “ሌላው TNT (Tin Nitro Toluen) ወይም ሳሙና ፈንጅ እያልን የምንጠራው ሲሆን ይህንንም በፈለግነው መጠን በመሰባበር ከቦታ ቦታ ልናንቀሳቅሰው እንችላለን፤ በተረፈ RDX፣ PTX፣ HMN፣ አሞኒየም ናይትሬት፣ TMX የመሳሰሉ ፈንጂዎችም በአገራችን የተገኙ ናቸው” ብለዋል፡፡ የአገራችን የፍተሻ መሳሪያዎች በአብዛኛው ብረት ነክ ነገሮችን የሚለዩ መሆናቸውን የገለፁት ኢንስፔክተሩ ፤ የጠቀስናቸው የፈንጂ ዓይነቶች ግን በአብዛኛው ከብረት ጋር ንክኪ ስለሌላቸው የሚያመልጡበት እድል መኖሩን በመጠቆም ትኩረትና ጥንቃቄ እንዲደረግባቸው አሳስበዋል፡፡

የአገራችን ህንፃዎች አሰራርም ለአደጋዎች የተጋለጡ መሆናቸውን ነው ሃላፊው የሚናገሩት፡፡ እዚህ አገር አጥፍቶ ጠፊዎች ባለመኖራቸው ነው እንጂ ህንፃዎቹ ለፍንዳታ ምቹ ናቸው፤ በቀላሉ በመኪና ላይ ወይም በመግቢያው በር ላይ ባሉ ምሰሶዎች ፈንጂዎችን በማጥመድ ጉዳት ማድረስ ይቻላል የሚሉት ኢንስፔክተር ታመነ፤ ህንፃዎቹን ከእንደዚህ ዓይነቱ አደጋ ለመታደግ የፕላን ስራ ላይ ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ ይመክራሉ፡፡ በፌደራል ፎሬንሲክ የፍንዳታ ምርመራ ዲቪዥን የፍንዳታ መሣሪያዎችን በቀላሉ በሚለዩና ፈጣን የምርመራ ውጤት በሚሰጡ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ትሩፋቶች የተደራጀ ሲሆን በብቃታቸው ለየት ከሚሉት ውስጥ ጥቂቶቹን እንያቸው፡፡ “ቫፐር ትሬሰር 2” “ቫፐር ትሬሰር 2” የተባለው መሣሪያ እጅግ ዘመናዊ እና ከፍተኛ ጠቀሜታ ያለው የቴክኖሎጂ ውጤት ነው፡፡ ይህ መሳሪያ ምንድን ነው? ለምንስ አገልግሎት ይውላል? “ቫፐር ትሬሰር”፤ በፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ዘርፍ ፎሬንሲክ ምርመራ ዳይሬክቶሬት ፍንዳታ ዲቪዥን ውስጥ ትልቅ አገልግሎት እንደሚሰጥ ኢንስፔክተር ታመነ ይናገራሉ፡፡

“ቫፐር ትሬሰር”ን የፈጠረው የአሜሪካ የሀገር መከላከያ እና የአደገኛ ዕፅ መቆጣጠሪያ ቴክኖሎጂ ዲፓርትመንት ሲሆን መሳሪያውን እየተጠቀሙበት ከሚገኙት አካላት መካከልም የአሜሪካ ጉምሩክ አገልግሎት፣ የፌደራል አቪዬሽን አስተዳደር፣ በፕሬዚዳንቱ ቢሮ የብሄራዊ አደገኛ እፅ ተቆጣጣሪ እና ሌሎችም የጥበቃና የደህንነት ባለሙያዎች ይጠቀሳሉ፡፡ በተጨማሪም በኤርፖርት፣ በኤምባሲ፣ በማረሚያ ቤቶችና ከፍተኛ ጥበቃና ክትትል በሚያስፈልጋቸው ቦታዎችና ተቋማት ይሄ መሣሪያ ጥቅም ላይ ይውላል፡፡ ከፍንዳታ በፊት በማንኛውም አጋጣሚ በተጠርጣሪዎች በተነካኩ እቃዎች ለምሳሌ ጠረጴዛ፣ የመኪና ማንኛውም አካል ፣ የቤት ውስጥ ዕቃዎች እንዲሁም ከሌሎች ነገሮች ላይ በቀላሉ ናሙና በመውሰድ ብቻ በመሳሪያው በመመርመር ወዲያውኑ ውጤቱን ማወቅ ይቻላል፡፡ ከፍንዳታ በኋላ ደግሞ ከተጎጂዎች አልባሳት ወይም ድንጋይ ላይ ናሙና በመውሰድና ምርመራ በማካሄድ ውጤቱን በአጭር ጊዜ ውስጥ ማወቅ እንደሚቻል ነው ኢንስፔክተሩ የሚናገሩት፡፡ በቀላሉ በእጅ ተይዞ የሚንቀሳቀሰው “ቫፐር ትሬሰር”፤ ክብደቱ 3.2 ኪ.ግ ሲሆን የተሰጠውን ናሙና ለመለየትም ከስምንት ሰከንድ እስከ አንድ ደቂቃ በቂ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡

መሳሪያው በፈንጅነት የተጠረጠረን ዱቄት መሰል ነገርና ስኳር እንዲሁም ቅባት መሰልና ከሌላም ነገር ጋር ተመሳሳለው ለፀረ-ሰላም ተግባር ሊውሉ የሚችሉ ፈንጅዎችን በቅፅበት እና በአስተማማኝ ሁኔታ በመለየት ውጤቱን ከማሳወቁ በተጨማሪም በማንኛውም አይነት እቃ ተጠቅልሎ የተቀመጠን ነገር በማሽተት በውስጡ ያለውን ነገር የመለየት አቅም አለው፡፡ በፋብሪካ ውስጥ በኬሚስትሪ ተቀምሞ የሚሰራን የፈንጅ አይነት ለይቶ በማሳወቅና የአደገኛ ዕፅ ዓይነቶችን በመለየት ረገድ መሳሪያው ትልቅ ጠቀሜታ ይሰጣል፡፡ ከፈንጅ አይነቶች TNT (Tin Nitro Toluen) ወይም ሳሙና ፈንጅ እያልን የምጠራውን እንዲሁም C4 (Composition four) ወይም ልቁጥ ፈንጅ፣ RDX፣ PTX፣ HMN፣ አሞኒየም ናይትሬትና TMX የተሰኙትን ጨምሮ ሌሎችም በአለም ላይ ያሉ በርካታ ፈንጅዎችን በቀላሉ ይለያል፡፡ “ኤኤል-6ዲ” ኤኤል-6ዲ (AL-6D) የሚባለው ዘመናዊ የኤሌትሮኒክስ መሳሪያ፣ ኤሌክትሮ ማግኔቲክ መልዕክት በፍጥነት በማስተላለፍና ቦታዎችን በመጠቆም የተዋጣለት ዘመኑ ያፈራው መሳሪያ ነው፡፡ ከተቀመጠበት ቦታ እስከ 20 ኪ.ሜ ርቀት 360 ዲግሪ በማካለል ጋራ፣ ህንፃ እና ምንም አይነት ከለላ ሳያግደው ፈንጅ፣ የጦር መሳሪያ፣ የሚፈነዳ ነገር፣ የኒውክለር አረር፣ ተተኳሽ ነገር፣ ባሩድ እና ማናቸውንም የሚፈነዱ ነገሮች ጨምሮ ማዕድንም መኖሩን በቅፅበት ማመላከት ይችላል፡፡

ምን ይሄ ብቻ … ወደ መሬት እስከ 8 ሜ. ጠልቆ በማንበብ የተጠቀሱት ነገሮች መኖራቸውን ለመግለፅም ጊዜ አይወስድበትም፡፡ ባህር፣ ውቅያኖስ፣ አሸዋማ ይሁን ኮንክሪት AL-6Dን አይበግረውም፡፡ ተሽከርካሪን ጨምሮ ባቡርም ይሁን መርከብ ላይ ጥቆማ ለመስጠት አይሳነውም፡፡ “ኤኤል-6ዲ” በቀላሉ በእጅ ተይዞ መንቀሳቀስ የሚችል ሲሆን ከኮምፒዩተር (ላፕቶፕ) ጋር በብሉቱዝ ተገናኝቶ በጎግል ኧርዝ አማካኝነት የተለያዩ መስመሮችን በማስመር ፈንጂው ወይንም ማዕድኑ የሚገኝበትን ቦታ ያሳያል፡፡ ከዚያም ወደ ቦታው በማምራት የተባለውን ነገር ማግኘት ይቻላል። እነዚህን ሥራዎች ያለ ምንም እንከን በማከናወን “ኤኤል-6ዲ” እጅግ የተዋጣለት በመሆኑ በርካታ የአውሮፓ ሀገሮችና ከሦስት የማይበልጡ የአፍሪካ ሀገራት መሳሪያውን እየተጠቀሙበት ይገኛሉ፡፡ ይህንን ዘመናዊ ኤሌክትሮኒክስ በአፍጋኒስታን፣ ፓኪስታንና ሌሎችም ፍንዳታ በሚበዛባቸው ሀገሮች ስራ ላይ አውለውት ባለውለታነቱን አስመስክሯል፡፡ “ኤኤል-6ዲ” ስቴድየሞችን፣ የአውሮፕላን ማኮብኮቢያዎችን፣ ወደቦችን፣ የአውቶብስ መናኸሪያዎችንና ሆቴሎችን እንዲሁም ሌሎች ቦታዎችን ከፍንዳታ አደጋ ነፃ እንዲሆኑ ፈጣንና ትክክለኛ መረጃ በመስጠት ከአደጋ የመጠበቂያ መሳሪያ ሆኗል፡፡

ይህንን መሳሪያ የሚሸጠው ዳዮድቢል ኮርፖሬሽን፤ ኤኤል -6ዲን “ለእያንዳንዱ ዜጋ የተፈጠረ ነፍስ አድን” በማለት ድንቅ የዘመናችን ቴክኖሎጂ መሆኑን ገልጿል፡፡ ይህንን ዋጋው እጅግ ውድና ጠቀሜታው ጉልህ የሆነውን የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያ ከሚጠቀሙበት ጥቂት የአፍሪካ ሀገራት መካከል ኢትዮጵያ አንዷ ነች። መሳሪያው በውድ ዋጋ ተገዝቶ በፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ዘርፍ ፎረንሲክ ዳይሬክቶሬት የፍንዳታ ዲቪዥን አማካኝነት አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ አገራችን ኤኤል 6ዲ ቴክኖሎጂን መጠቀም በመጀመሯ ቢሮ ውስጥ ቁጭ ብሎ በ20 ኪ.ሜ ርቀት ሊፈነዱ የሚችሉ ነገሮችን መቆጣጠር ተችሏል፡፡ መንግስታትና ትልልቅ ባለስልጣናት በሚንቀሳቀሱበት ወቅት፣ መንግስታዊና ህዝባዊ ስብሰባዎች፣ እግር ኳስ ጨዋታዎችና የሃይማኖት በዓላትና ሌሎችም እንቅስቃሴዎች በሚኖሩበት ጊዜ መሳሪያው ያለ ምንም ስጋት እንዲከናወን ያስችላል፡፡ በኤርፖርቶችና ሌሎችም ቦታዎች ቢሆን አስተማማኝ በሆነ ሁኔታ የፍንዳታ ስጋትን ማስወገድ ተችሏል ብለዋል - ኢንስፔክተር ታመነ፡፡

Published in ህብረተሰብ

“ቢግ ብራዘር” ወንድም ጋሼ እንደማለት ነው፡፡ በዲኤስ ቲቪ የሚተላለፈው ይሄ የቲቪ ሪያሊቲ ሾው የሚቀርበው ከዓለም ተገልለው በአንድ ቤት ውስጥ በደባልነት የሚኖሩ ወጣቶችን እንቅስቃሴ ለ24 ሰዓት በካሜራ በመከታተል ነው፡፡ ፉክክሩ ለሶስት ወር የሚቆይ ሲሆን ሳይባረር የተመልካቾችን ይሁንታ (ድምጽ) እያገኘ እስከመጨረሻው ድረስ የዘለቀ ተወዳዳሪ እስከ 300ሺ ዶላር የሚደርስ ሽልማት ያገኛል፡፡ የአፍሪካ “ቢግ ብራዘር” አስራ አራት አገሮችን ያሳትፋል፡፡ የመጀመርያው ውድድር (እ.ኤ.አ በ2003 ዓ.ም) አንጎላ፣ ቦትስዋና፣ ጋና፣ ኬንያ፣ ማላዊ፣ ናምቢያ፣ ናይጀርያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ታንዛንያ፣ ኡጋንዳ፣ ዛምቢያ እና ዚምባብዌ የተካተቱበት ሲሆን በአራተኛ ዓመት ውድድሩ ደግሞ ኢትዮጵያ እና ሞዛቢክን ጨምሯል፡፡ በሰባተኛው ዓመቱ ላይ ላይቤርያ እና ሴራሊዮን ተካትተዋል፡፡ ወንድም ጋሼ እና ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ ለመጀመርያ ጊዜ የዚህ ትርኢት አካል የተደረገችው በ “ቢግ ብራዘር” አራተኛ የውድድር ዘመን ያእቆብ አቤሴሎም በተባለ ወጣት አማካኝነት ነበር፡፡

ይህም እ.ኤ.አ. በ2009 ዓ.ም መሆኑ ነው፡፡ ቀጣዩ የትርኢቱ ዘመን ከዚህ በፊት በትርኢቱ ተሳታፊ የነበሩ ሰዎች ተመልሰው የተወዳደሩበት ሲሆን ያእቆብ ዳግም ከኢትዮጵያ ተሳትፏል፡፡ ያእቆብ እና አጋሩ በአራተኛው የውድድር ዘመን ለሳምንት ያህል በረት ውስጥ እንዲኖሩ የቀረበላቸውን ፈተና ያዕቆብ መቋቋም ባለመቻሉ ከውድድሩ እራሱን አግሏል፡፡ በቀጣዩ የውድድር ዘመን ኢትዮጵያ፣ ዳኒ እና ሃኒ በተባሉ ወጣቶች ተወክላ ተሳትፋለች፡፡ በሰባተኛው ዘመን ኢትዮጵያ ተሳትፎ አልነበራትም፡፡ አሁን በስምንተኛው የውድድር ዘመን ደግሞ ይህን ጽሑፍ ለማዘጋጀት ሰበብ የሆነችኝ ቤቲ የተባለች የ26 ዓመት ወጣት መምህርት ተወክላለች፡፡ ይህን ጽሑፍ በቤቲ ምክንያት ለመፃፍ ብነሳሳም ዓላማዬ ቤቲ ላይ በማነጣጠር እሷን መውቀስ አይደለም፡፡

እሷ የዚህ አፀያፊ ተግባር አካል እንድትሆን ተደርጋለች ብዬ አምናለሁ፡፡ ዋናው ግቤ ግን ስለ ትርኢቱ ሰፊ መረዳት እንዲኖረንና ለወደፊቱ ከዚህ ሞኝነት እራሳችንንና ሃገራችንን የምንጠብቅበት አስተዋይነት እንዲኖረን ማድረግ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር በሚቀጥለው ዓመት ትርኢቱ ወደ ሃገራችን ለምልመላ ሲመጣ ፍቃድ ነስቶ ማባረርና ከአሁኑ ሰዓት ጀምሮ ደግሞ በሐገራችን ፕሮግራሙ እንዳይሰራጭ ግፊት ማድረግ ነው፡፡ በተረፈ ለቤቲ መልካሙን ሁሉ እንዲገጥማት በመመኘት ውድድሩ ሲጠናቀቅ ተመክሮዋን ለመላው ዓለም ታጋራ ዘንድ ፍላጎቴ ነው፡፡ እሷ ለእኔ የፕሮግራሙ ሰለባ እንጂ ሌላ አይደለችም፡፡ አንድ ጥያቄ ጣል አድርጌ ልለፍ፡፡ እቺ ወጣት ፈፀመች የተባለውን የፈፀመችው ወዳና ፈቅዳ ወይስ በተፅእኖ ይሆን? ጋጠወጥነት ከወንድም ጋሼ እስከዛሬ ይሄ የሪያሊቲ ሾው ፕሮግራም ምን ዓይነት ጋጠወጥ ክስተቶችን አስተናግዷል የሚለውን ደግሞ መረጃ እየነቀስን እንመልከት፡፡

በተለይ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች በ”ቢግ ብራዘር” ውድድሮች አማካኝነት የተፈፀሙ ቅሌቶችን ለማሳየት እሞክራለሁ፡፡ አፍሪካ፣ 2003 ወንድም ጋሼ በአፍሪካ የመጀመርያ የውድድር ዘመኑ ነበር ውዝግብ ያስነሳው፡፡ የዩጋንዳው ተወዳዳሪ ካግዋ እና የደቡብ አፍሪካዋ ፕሌትጀት በቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭቱ ወሲብ እያደረጉ ያለ የሚመስል ነገር ታይቶ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በወቅቱ ፕሮግራሙ በማላዊ እንዲቋረጥ ተደርጎም ነበር፡፡ ብራዚል፣ 2012 ሞኒክ የተባለች ተፎካካሪ ሰክራና እራሷን ስታ አልጋዋ ውስጥ ተኝታ ሳለ፣ ዳንኤል የተባለ ተፎካካሪ የእሷን ይሁንታ ሳያገኝ አልጋው ውስጥ ገብቶ ወሲብ በመፈፀሙና እሷም “ያለ ፈቃዴ የተፈፀመ” ነው በማለቷ፣ ክብረ ንጽህናዋን (ውድድሩ ውስጥ ሲገቡ ክብር የሚባል ነገር የለም) ገስሷል ተብሎ ወዲያውኑ ከውድድሩ ተባርሯል፡፡ አሜሪካ፣ 2001 ጀስቲን ሴቢክ የተባለው ተወዳዳሪ ክሪሳት ስቴጋል የተሰኘችውን ሌላ ተወዳዳሪ ቢላ አንገቷ ስር ይዞ እያስፈራራ ሲስማት የታየ ሲሆን ይህም ተፎካካሪ ወዲያውኑ ከፕሮግራሙ እንዲባረር ተደርጓል፡፡

አፍሪካ፣ 2008 ታዋና ሌባኒ የተባለች ተፎካካሪ ታኮንዳዋ ንኮንጄራ የተባለ ተፎካካሪን ብልት በአፏ ስትነካካ ታይታለች፡፡ ይህችው ሴት ከሁለት ወንዶች ጋር የተኛች ሌላ ተፎካካሪን “ሰይጣን” ብላ ያወገዘቻት ቢሆንም እሷ ራሷ ከሁለት ተወዳዳሪ ወንዶች ጋር በአንድ ግዜ ወሲብ መፈፀሟ ተዘግቧል፡፡ ከውድድሩ ተሸንፋ ስትወጣም የሃገሯን የቦትስዋና ባንዲራ ለብሳ “ብልት እወዳለሁ!” በማለት በቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት አውጃለች፡፡ ታዲያ ከዚህ በላይ ምን ቅሌት ይኖራል? አውስትራሊያ፣ 2005 ማይክል ብሪክ እና ማይክል ኮክስ የተባሉ ተወዳዳሪዎች በፈጸሙት ወሲባዊ ጥቃት ከትርኢቱ ተባርረዋል፡፡ በዚህ ውድድር ብሪክ የተባለው ተፎካካሪ ካሚላ ስቭሪ የተባለች ተወዳዳሪን በጉልበት ከያዛት በኋላ፣ ኮክስ የተባለው ሌላ ተወዳዳሪ ብልቱን ፊቷ ላይ ሲያደርግ በቀጥታው ስርጭት ታይቷል፡፡ በወቅቱ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ጆን ሃዋርድ፤ የፕሮግራሙ አስተላላፊ የነበረው “ቻነል 10” ይህን “ጅላንፎ” ፕሮግራም ማስተላለፍ እንዲያቆም ጠይቀው የነበረ ቢሆንም ትርኢቱ ግን እስከዛሬ ቀጥሏል፡፡

ብሪታንያ፣ 2005 ኪንጋ ካሮልክዛክ ወጣ ባለ ጋጠወጥ ባህሪዋ (በዋሾነት፣ ሰካራምነትና እርቃኗን በመሆን) በትርኢቱ ገንና ከቆየች በኋላ፣ በፉክክሩ አጋማሽ ላይ እጅግ ወጣ ያለ ድርጊት ፈፅማለች፡፡ እንደልማዷ ሰክራ እግሯን ከፍታ ተንጋላ ከተኛች በኋላ፣ ባዶ የወይን ጠርሙስ ተጠቅማ እራሷን ለማስደሰት ስትሞክር ታይታለች፡፡ ኮሮልክዛክ ከውድድሩ በኋላ ለ “ዴይሊ ሚረር” በሰጠችው ቃለምልልስ ድርጊቱን የፈፀመችው ከፕሮግራሙ ባለቤቶች በቀረበላት መደለያና በደረሰባት “ትባረርያለሽ” የሚል ማስጠንቀቂያ የተነሳ እንደሆነ ተናግራለች፡፡ አፍሪካ፣ 2007 አልኮል ያለመጠን የወሰዱት ሪቻርድ ቤዙዴንሃውትና ኦፋኔካም ተመሳሳይ ጋጠወጥ ድርጊት እንደፈፀሙ ተዘግቧል፡፡ ሪቻርድ እራሷን ስታ ከተኛችው ኦፉኔካ አጠገብ በመተኛት በእጆቹ ብልቷን ሲደባብስ የታየ ሲሆን ሌላ ተወዳዳሪ ሴት የሚሰራውን እንዲያቆም ስትጮህበት ነበር ከድርጊቱ የተገታው፡፡ ይህ አሰቃቂ ድርጊት በቲቪ በቀጥታ እየተሰራጨ የነበረ ሲሆን እዚህ ጋ ሲደርስ እንዲቋረጥ ተደርጓል፡፡

ወዲያው የህክምና እርዳታ አድራጊዎች ለተወዳዳሪዋ የደረሱላት ቢሆንም ድርጊቱ የአስገድዶ መድፈር ሙከራ መሆኑ እየታወቀ ጣቢያው “በፈቃዷ የተፈፀመ ነው” በሚል ትርኢቱ እንዲቀጥል አድርጓል፡፡ በመጨረሻም የአስገድዶ መድፈር ሙከራ ፈፃሚው አንደኛ፣ ተደፋሪዋ ሁለተኛ ወጥተው ፉክክሩ ተጠናቋል፡፡ ዘንድሮ ደግሞ ኢትዮጵያዊቷ ቤቲ ወሲብ ስትፈጽም ታይቷል፡፡ የአፍሪካ ወጣቶች ጋጠወጥ ድርጊቶችን የሚያሰራጨው የዲኤስቲቪው ኤምኔት ቻናል ሃይ ባይ ያጣ ይመስላል፡፡ እንደ ማላዊ ያሉና የናይጄርያው ኤንቢሲ ቴሌቪዥን ፕሮግራሙ እንዳይተላለፍ እገዳ ጥለውበት እንደነበር ይታወቃል፡፡ የወንድም ጋሼ ፋይዳ ምንድነው? የብሪታንያው ጎልድስሚዝ ዩኒቨርሲቲ፣ የስነ ማህበረሰብ ፕሮፌሰር የሆኑት ቤቨርሊ ስኬግስ፤ [የትርኢቱን] ቅርጽ የማህበረሰቡ የኃይል አወቃቀር ከማህበራዊ ለውጥ ጋር እንዲለወጥ የሚያደርግ፣ የሰዎች ስብእናና ተግባሮቻቸው በጥሩ እና መጥፎ ምድቦች የሚከፋፈሉበት የግምገማ መንገድ ነው ይሉታል፡፡ አንዳንድ ወገኖች ደግሞ ይሄን ፕሮግራም እንደ አንድ አፍሪካዊ ባህል መፍጠርያ መድረክ ይቆጥሩታል፡፡

ለእኔ ግን አፍሪካውያንን ከእነ ባህላቸው የሚያጠፋ መድረክ ነው፡፡ ይህ ጽሑፍ የተጻፈው በወግ አጥባቂ ግለሰብ ነው፤ በሚል ግምት እውነታውን አያሳይም የሚል ካለ እጅጉን ተሳስቷል፡፡ ከቀረበው መረጃ አንጻር ማንኛውም ሰብአዊ ክብሩን፣ መንፈሳዊ ሰላሙንና ነጻነቱን የሚወድ ሰው ሁሉ፣ ከዚህ ጋጠወጥ ምግባር እራሱንና የሚቆረቆርለትን ወገን ሊጠብቅ ይገባል ብዬ አምናለሁ፡፡ ይሄ ጋጠወጥ የቲቪ ፕሮግራም በአገራችን እንዳይሰራጭ፣ ወጣቶችም በውድድሩ ከመሳተፍ እንዲቆጠቡ ቤተሰቦች፣ ሚዲያዎችና ያገባናል የሚሉ ወገኖች ሁሉ የበኩላቸውን ጥረት ያደርጉ ዘንድ እማፀናለሁ፡፡ ሥርጭቱን ከማሳገድ መለስ ያለው ሌላው አማራጭ ደግሞ መረጃን በመረጃ መታገል ነው። የሕዝብ ግንኙነት አባት እየተባለ የሚወደሰው ኤድዋርድ በርኔይስም፤ “የፕሮፓጋንዳ ምርጡ መመከቻው፣ ተጨማሪ ፕሮፓጋንዳ ነው” ብሏል። ያለዚያ ግን እንዲህ ያለው ጋጠወጥ ፕሮግራም የባህልና የማንነት ቀውስ መፍጠሩ ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡

Saturday, 22 June 2013 11:04

ጭፈራችንን መልሱልን

ኩርማን መግቢያ
እግዜር ከሞላው ኩሬ ውስጥ ፣ እስቲ እንዋኝ ብለን ገብተን
ሳንጨርሰው ውሃው ደርቆ፣ መካከል ላይ ዋጋ ከፈልን!
ለኩሬ ዋናው ተጥፈን
በውቂያኖሱ ተቀጣን!
***
አለሥራችን ገብተን፣ አንጨቅጭቀው እግዜአብሔርን፤
ይቅርታ እንጠይቅ እንጂ፣ ስለመፈጠራችን፤
ለመኖሪያችንማ፣ “የቀን ውሎ - አበል” አልን!
ተጠባባቂ ቤንች እንጂ፣ ቋሚ ተሰላፊ አደለን!
የካምቦሎጆን ነገር፣ የቀመሰ ያቀዋል
ለካስ ኳስ ሳይሞቁት በፊት፣ ጨዋታው ብርድ - ብርድ ይላል፡፡
***
ጭፈራችንን መልሱልን
ያገር ብርድ ሲቆነድደን
ኳስ ሜዳውን አልቤርጐ አርገን
ድንጋይ ጠርዙን ተንተርሰን
የታክሲ ውስጥ አልጋ አንጥፈን
ሌት በዋዜማ አልመን፣ ነገን በዕውነት ልናበራ፤
ባንዲራ እንደደመራ
ከምረን በየኳስ ጐራ፤
ተውለብልበን አውለብልበን
ላንቃችን እስኪበጣጠስ፣ ሆ ብለን በማታ በቀን፤
በጭለማ ድል ጐስመን
አገር ላዕላይ ነው ብለን፤
የሰው እግር እንደጅረት፣ ጨርቅ ማሊያው እንደጐርፍ
ባንዲራውን እንደ ጅራፍ
ስናጮኸው መኪና አፋፍ፤
በጥሩምባ መለከት አፍ
የሳግ ጩኸት ሞታችንን
ስናንባርቅ ድላችንን፣
ያን መሳይ ዝማሬ ቃና፣ ያን ጭፈራ ታስነጥቁን?!
እግዜር ለድል እያበቃን፣ እኛው “የእግዜር ስተት” ከሆን
ከመዋል ከማደር በቀር፣ ለህይወትም ያው “ቤንች” ነን!!
አዬ መጥኔ ካምቦሎጆ
አድሮ የንፍገት ኮሮጆ!
በሠርግ አጋፋሪ ጥፋት፣ ከፈረሰ ድንኳን ዳሱ
ገና ሜዳ ሳንገባ፣ ከተነፈሰማ ኳሱ፤
ለምን ላገር ይትረፍ ጦሱ?
ጭፈራችንን መልሱ!!
እናንተው ተከሳሰሱ
ብቻ ሳትውሉ ሳታድሩ፣ ጭፈራችንን መልሱ!!
ሰኔ 11/2005 (ለምስኪኑ ህዝባችን)

 

Published in የግጥም ጥግ

ከዕለታት አንድ ቀን የዱር አራዊት አያ አንበሶ ከበሽታቸው መዳናቸውን ምክንያት በማድረግ ድግስ እንዲደገስ ተስማሙ፡፡ አያ አንበሶም ፈቀዱ፡፡ በቅደም - ተከተል ባለሟሎቹ ስማቸው ተዘረዘረ ተፃፈና ጮክ ተብሎ ተነበበ፡፡

“አንደኛ - ነብሮ” ተባለ፡፡ ተጨበጨበ፡፡ “ሁለተኛ - አያ ዝሆን” ተባለ፡፡ ተጨበጨበ፡፡

“ሦስተኛ - አውራሪስ” ተባለ ተጨበጨበ፡፡

“አራተኛ - አጋዘን” ቀጠለ ተጨበጨበ፡፡

“አምስተኛ - ጅብ” ተጨበጨበ፡፡

“ስድስተኛ - ዝንጀሮ” እያለ ግንባር ግንባር ቦታ፤ ዋና ዋና ወንበር ላይ የሚቀመጡቱ በዝርዝር ታወቁ፡፡ አያ አንበሶ ቀጠሉና፤ “ታምሜ ያልጠየቁኝ ወደዚህ ድግስ እንዳይመጡ” ሲሉ አስጠነቀቁ፡፡

አክለውም “በተለይ ጦጣ!” አሉ፡፡ በዚሁ መሠረት ለሁሉም አራዊት የድግሱ ጥሪ እንዲደርሳቸው ተባለና ተላከባቸው፡፡ ድግሱ ድል ተደርጐ ተደግሷል፡፡ ያልተጠራ የዱር አራዊት የለም፡፡ አሰላለፋቸው የታወቀ ነው፡፡ አንበሳ ሁሉንም በደምብ በሚያይበት ዙፋን - አል ወንበሩ ላይ ኮራ ብሎ ተቀምጧል፡፡ እነ ነብር፣ እነዝሆን፣ እነ አጋዘን፣ እነድብ ወዘተ በየተከታታይ ተርታ ተሰድረዋል፡፡ ጦጢት የለችም፡፡ ምክንያቱም አያ አንበሶ ታመው፤ አንድ ሁለት ጊዜ አጭበርብራ ሳትጠይቃቸው በመቅረቷ ነው፡፡ ካዩዋት አይለቋትም፡፡ ሆኖም የተለየ ልብስ ለብሳ ዋና አጋፋሪ ሆና ድግሱን ስታሞቀው ውላለች፡፡

“እዚህ ድግስ ተጠርተሻል? እንዴ?” ሲል ከተጋባዦች አንዱ ጠየቃት፡፡ ውስጥ አዋቂ ብጤ ነው፡፡ “ኧረ አልተጠራሁም” አለች ጦጢት “ታዲያ ምን ታረጊ መጣሽ?” አላት ሌላው፡፡ “ዘመዶቼ ቅር እንዳይላቸው ብዬ ነው” “ኋላ አያ አንበሶ ቢያገኙሽና አንድ ቅጣት ቢቀጡሽስ? ፀፀቱ ለዘመዶችሽ አይሆንም ወይ? ደሞም ታላላቅ ዘመዶችሽ ውርደቱን አይችሉትም፡፡ መዘዝሽ ለሁሉ ይተርፋል፡፡ “እግዜር ጥሎ አይጥለኝም፡፡ ድፍረቱን ሰጥቶ ከድግሱ ከቀቀለኝ፣ ከእሳቱ መውጪያውንም እሱ ያበጅልኛል፡፡” ሁሉም ተሳሳቁ፡፡ ከመሀል አንደኛው፤ “አይ ጦጢት፤ ዱሮ በብልጠቷ ነበር የምትተማመነው፡፡ አሁን ለአምላክ እጇን ሰጠች፡፡ አይ ጊዜ! ጊዜ ሁሉን ያጋልጣል፡፡ ጦጢትንም ቢሆን” አለ፡፡

                                                        ***

ሁሌ ብልጠት አያዋጣም፡፡ “አፍና ቅብቅብ ሁልጊዜ አያበላም” ይላሉ አበው፡፡ በብልጠት ሸፋፍኖ ዛሬን ማለፍ ይቻል ይሆናል፡፡ ነገ ግን ብልጠቱ ያረጅና ዕውነቱ እንደአዲስ ቆዳ ብቅ ይላል፡፡ ስለዚህ “ሞት ላይቀር ማንቋረር” ነው የሚሆነው፡፡ የሀገራችን እስፖርት የብዙሃን መዝናኛና የብዙሃን መፎካከሪያ ነው፡፡ ውስጥ፣ እርስ በርሱ እንደየቲፎዞው አቅም ይሟገታል፡፡ ይወራረዳል፣ ይጋጫል፡፡ ከውጪ ቡድን ጋር ግጥሚያ ሲመጣ ግን ብዙሃኑ ህዝብ የእርስ በርስ ፉክክሩን፣ ፉክቻውንና፣ ሽኩቻውን ወደጐን ትቶ የአገር ጉዳይ ነው ብሎ፤ ሥጋውንም ነብሱንም ይሰጣል፡፡ ሲሸነፍ ደግሞ ፀጉሩን ይነጫል፤ አንጀቱ ያርራል፡፡ ሲያሸንፍ ዘራፍ ይላል፡፡ ያምባርቃል፡፡ መንገድ ይሞላል፡፡ የሞተር ብስክሌት አክሮባት፣ የመኪና ሰልፍ፣ የሰው ጐርፍ… ድብልቅልቁ ይወጣል፡፡

ደስታና ሁካታው ጣራ ይነካል! (The sky is the limit እንዲሉ ፈረንጆች) አንድ ክስተት የአገር ጉዳይ ሲሆን ህዝብ ከአፍ - እስከ ገደፉ እንደሚንቀሳቀስ መገለጫው እንዲህ ያለው የስፖርት ስሜት ነው፡፡ ነፍሱን - ልቡን ገብሮ የሚቆምለት ስሜት ነው!! ይህን ስሜት ማጭበርበር አይቻልም፡፡ ይህን ስሜት ማውገርገርና ማኮላሸት ክፉ ቁጣ፣ ሐዘንና ክፉ ፀፀት ይፈጥራል፡፡ ብርድ እየፈደፈደው፣ እንቅልፉን አጥቶ የጮኸለትን ድሉን በተራ ስህተት ሲነጠቅ ማየት እጅግ አሳዛኝ ነው፡፡ ስህተቱ የማንም ይሁን የማን አስተምሮ፣ አስምሮ፣ አመሳክሮ የመገኘትን ቁብ አጉልቶ አሳይቷል፡፡

“አንተ እኮ የእግዜር ስህተት ነህ” እንዳለው ነው ፀሐፌ - ተውኔቱ፤ በንዴት ስናጤነው፡፡ ዞሮ ዞሮ ዋና ዋና ቁቦቻችንን ብንነቁጥ:- አገር ድብብቆሽ መጫወቻ፣ አየሁሽ አላየሁሽ መባባያ አይደለችም! ስህተትን መወያየት እንጂ መደባበስ የትም አያደርሰንም፡፡ ይቅርታ መጠየቅ ክቡር ባህል ነው፡፡ ኃላፊነትን መቀበል የሰለጠነ መንገድ ነው፡፡ ውስጣችንን መፈተሽ፣ መረጃዎቻችንን በጥብቅ መያዝ፣ በየትንሹ ጉዳይ አለመበርገግ፣ አለመዝረክረክ ዋጋ ከመክፈል ያድናል፡፡ በመጨረሻም ህዝብ የጮኸልንን ያህል የጮኸብንና የተነሳብን ቀን ወዮልን ማለት አይቀሬ መሆኑን መገንዘብ የብስለት ምልክት ነው፡፡ አመንነውም አላመንነውም፤ መዘንነውም ሸቀብነውም፤ አስፈላጊውን ቅድመ - ሁኔታ ሳናሟላ ሜዳ ውስጥ መገኘት፤ “እንሥራዋን ጥላ ወንዝ ወረደች” እንደሚባለው ተረት መሆኑ የነገሩ ብልት ነው!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

ዶ/ር ነጋሶ የመጀመሪያው ፈራሚ ሆነዋል

“የአገሩን በሬ በአገሩ ሰርዶ እንጂ በውጭ ተቋማት መተማመንይቅር” - ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማሪያም

አንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ (አንድነት) ከትላንት በስቲያ በይፋ የጀመረው ህዝባዊ ንቅናቄ የፀረ-ሽብር አዋጁን ማሰረዝ ዋነኛ አላማው እንደሆነ ገለፀ፡፡ ለዚህ ዓላማውም የአንድ ሚሊዮን ሰዎችን የድጋፍ ፊርማ (ፒቲሽን) በዕለቱ ማስፈረም የጀመረ ሲሆን የመጀመሪያው ፈራሚ የፓርቲው ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ሆነዋል፡፡ ፓርቲው የፀረ-ሽብር ህጉን ለማሰረዝ ከሚንቀሳቀስባቸው ምክንያቶች አንዱ ህገ-መንግስቱን በእጅጉ የሚጥስና የኢትዮጵያን ዜጐች በማጥቃት የሚጀምር በመሆኑ ነው ብሏል - የህዝባዊ ንቅናቄው ኮሚቴ በሠጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፡፡

ፓርቲው “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል መሪ ቃል የጀመረው የሶስት ወር ንቅናቄ የአንድ ሚሊዮን ህዝቦችን ድምፅ በማሰባሠብ የአገሪቱን ዜጐችና ተቋማትን በማጥቃት፣ በሀይማኖት ጣልቃ በመግባት፣ ከአባትና እናት የተወረሠን ንብረትና ሀብት በሽብርተኝነት ስም የሚገፈውን አዋጅ ለማሰረዝ ጥረት እናደርጋለን፤ ወደ ክስም እንሄዳለን” ብሏል፡፡ “ይህ ማለት ግን ኢትዮጵያ ካላት ተፈጥሯዊ ሀብትና መሠል ጉዳዮች ጋር በተያያዘ የፀረ-ሽብር ህግ አያስፈልጋትም ማለት እንዳልሆነ የገለፁት የንቅናቄው ኮሚቴ አባል አቶ ትዕግስቱ አወል፤ አሁን ስራ ላይ ያለው የፀረ ሽብር አዋጅ ግን ሰዎችን እና ተቋማትን የሚያጠቃ ነው ብለዋል፡፡

ከተጠቁት ተቋማት ውስጥ አንድነትና መድረክ ዋነኞቹ እንደሆኑ፣ ጋዜጠኞችና የፖለቲካ ሰዎችም የዚሁ አዋጅ ሠለባ መሆናቸውን፣ እንዲሁም ከህገ መንግስቱ ጋርም በከፍተኛ ሁኔታ ስለሚቃረን ትኩረት አድርገንበታል ሲሉም አክለዋል፡፡ “ምንም እንኳን በፍትህ ተቋማቱ ላይ ያለን እምነት የተሸረሸረ ቢሆንም አሁንም መብታችንን ከመጠየቅ የሚያግደን የለም” ያሉት የንቅናቄው ኮሚቴ አባል አቶ ዳንኤል ተፈራ፤ መንግስት የ1 ሚሊዮን ሠው ድምፅና ጥያቄ አልቀበልም ካለ የፓርቲውን ሳይሆን የህዝቡን ጥያቄ አልመልስም እንደማለት እንደሆነ አብራርተዋል፡፡

ፓርቲው በሶስት ወሩ ህዝባዊ ንቅናቄ ውስጥ ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚካተት ገልፆ፤ በዋናነት ህገ-መንግስቱን የሚፃረረውን የፀረ ሽብር አዋጅ ማሰረዝ፣ በአገር አቀፍ ደረጃ እየተካሄደ ያለውን በገጠርና በከተማ የዜጐች መፈናቀልና የመሬት ቅርምት ማስቆም፣ የስራ አጥነትና የኑሮ ውድነት እንዲቀረፍ ማድረግ፣ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ማሻሻያ እርምጃ እንዲወሠድና የንግዱ ማህበረሠብ ከወንጀለኝነት ስምና ስግብግብ ከመባል ወጥቶ ጤናማ ውድድር እንዲኖር፣ እንዲሁም ማጥላላትና ማዋከብ እንዲቆም ማድረግ የሚሉት በዋናነት ተቀምጠዋል፡፡ የንቅናቄው ኮሚቴ አባል የሆኑት አቶ ተክሌ በቀለ፤ ንቅናቄው አሁን የተጀመረበትን ምክንያት ሲያብራሩ፤ “እስከዛሬ ንቅናቄውን ያልጀመርነው ፓርቲው በአየር ላይ የተንጠለጠለ እንዳይሆን በእግሩ እንዲቆም በማድረግ ስራ ላይ እና በውስጥ አደረጃጀት ተጠምደን ስለነበር ነው” ብለዋል፡፡

“እስከዛሬ እግር ሲያወጡ እንቆርጣቸዋለን እየተባለን፣ እግር ስናወጣና ስንቆረጥ ቆይተናል” በማለት ያከሉት አቶ ተክሌ፤ አሁን ግን በኢህአዴግ የሚደርስብንን ብቻ ሳይሆን የውስጥ ህመማችንንም ስናክም ቆይተን ከጨረስን በኋላ በእውቀት ላይ የተመሠረተ የህዝብ ንቅናቄ ለመጀመር ጊዜው አሁን እንደሆነ ውሳኔ ላይ ደርሰናል ብለዋል፡፡ “በፍ/ቤቶች ላይ እምነታችን ቢሸረሸርም ፍትህ መጠየቃችንን አናቆምም” ያሉት አቶ ዳንኤል፤ የአንድ የሚሊዮኖችን ድምፅ የምናሠባስበውም ለዚሁ ነው ብለዋል፡፡

ዶ/ር ሀይሉ አርአያ በሠጡት አስተያየት አንድ አካል አጥፍቶ ያለመጠየቅን ነገር ፈረንጆቹ (Impunity) ይሉታል” ካሉ በኋላ “እዚህ አገርም አጥፍቶ የሚጠየቅ የለም፤ ስለዚህ በአገራችን ፍ/ቤት ካልተሳካ ወደ አለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት የሚኬድበት አማራጭም መዘንጋት የለበትም” ብለዋል፡፡ ነጋዴዎችን በተመለከተ ለተነሳው ጥያቄ “የዚህን አገር ነጋዴዎች ለማወቅ የግድ የመጫኛ ነካሽ ልጅ መሆን አያስፈልግም” በማለት ምላሽ መስጠት የጀመሩት የንቅናቄው ኮሚቴ አባል አቶ አቶ ዳዊት ሰለሞን፤ በአሁኑ ሰዓት ነጋዴው ሌባ፣ ዘራፊ፣ ሙሰኛ እየተባለና እየተብጠለጠለ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ “ገዢውን ፓርቲ የተጠጉ አካላት በአንድ ጀምበር የሀብት ማማ ላይ ሲወጡ፣ በህጋዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ነጋዴዎች በስቃይ ላይ ናቸው ያሉት አቶ ዳዊት፤ የጥሬ እቃ እጥረትና መሠል ችግር ሲፈጠር መንግስት ጣቱን በነጋዴ ላይ እንደሚቀስር ጠቁመው፣ ነጋዴው በአገሩ አንገቱን ደፍቶ እንዲኖር የሚደረግበት አካሄድ እንዲቆም እንጠይቃለን ብለዋል፡፡

Published in ዜና
  • ጉዳዩ የቡድን መሪውንና አሰልጣኙን ተጠያቂ እንደሚያደርጋቸው ተገለፀ
  • ጥፋተኛ ሆነው ከተገኙ ከ6 ወር እስከ 10 አመት በእስር ሊቀጡ ይችላሉ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለአለም ዋንጫ ማጣሪያ ከደቡብ አፍሪካ አቻው ጋር ተጫውቶ ያስመዘገበው ሶስት ነጥብ በፊፋ ውሳኔ መቀነሱን ተከትሎ ብዙዎችን እያነጋገረ ያለው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ስህተት፣ በወንጀልና በፍትሀብሔር ህግ ያስጠይቃል ሲሉ የህግ ባለሙያዎች ተናገሩ፡፡ በወንጀል ህጉ አንቀጽ 702 እና 703 ላይ የተረከቡትን ስራ በአግባቡ አለመወጣት እና ቸልተኝነት ወይም አውቆ አለማድረግ እንደሚያስከስስ የተናገሩት የህግ ባለሙያው አቶ ፈቃዱ ፀጋ፤ የቡድን መሪው እንደተባለው ከጉዳዩ ጋር የሚያያዘው ደብዳቤ ደርሶት ተገቢውን እርምጃ ሳይወስድ ከቀረ ሃላፊነቱን ባለመወጣት ተጠያቂ ይሆናል ብለዋል፡፡

አሠልጣኙም የስራ ዝርዝር ሃላፊነታቸው ላይ የተቀመጠውን ነገር በአግባቡ ካልፈፀሙ ተጠያቂ ይሆናሉ የሚሉት አቶ ፍቃዱ፤ በወንጀለኛ ህጉ አንቀፅ 58 1 (ሀ) እና (ለ) “ቀጥታ ቸልተኝነት” ወይም ደግሞ “የሆነ ይሁን ብሎ” የሚል ሲሆን፣ ሃላፊው “የሆነ ይሁን” ብሎ፣ “ቅጣት ቢመጣም ይምጣ” በሚል ማሳለፍ ፈልጐ ካደረገ ወይም የተቀጣን ለይቶ ማሰለፍ ሲገባው ባለማድረጉም ለሰራው ስራ ሁለቱም በዚህ አግባብ ሊጠየቁ እንደሚችሉ ገልፀዋል፡፡ ይሄ አንቀጽም ከ 6ወር -10 አመት የሚያስቀጣ መሆኑን ገልፀው፤ ከዚህ በኋላም አገሪቱ ያጣችውን በፍትሀብሔር መጠየቅ ትችላለች ብለዋል፡፡ ሌላው የህግ ባለሙያ አቶ ደበበ ኃ/ገብርኤል በበኩላቸው፤ በጉዳዩ ሰበብ የሚደርስ በገንዘብ የሚተመን ጥቅም ከቀረ ሙያዊ ሀላፊነት በአግባቡ ባለመወጣት እና በአስተዳደራዊ እርምጃ ሊጠየቁ ይችላሉ ብለዋል፡፡

የገንዘብ ጥቅምን በተመለከተ በፍትሐብሔር መጠየቅ ይቻላል የሚሉት አቶ ደበበ፤ አስተዳደራዊ እርምጃን በተመለከተም ከስራ ማሰናበትና ሌሎች አስተዳደራዊ እርምጃዎችን መውሰድን እንደሚያካትት ገልፀዋል፡፡ ድርጊቱ የተፈፀመው በከፍተኛ ቸልተኝነት ከሆነ ደግሞ በወንጀል ሊጠየቁ ይችላሉ ያሉት አቶ ደበበ፤ በሚከሰሱበት የወንጀል አይነቶች እንደየደረጃቸው ሊቀጡ እንደሚችሉም ተናግረዋል፡፡ የተሰጠን ሃላፊነት በቸልተኝነት አለመፈፀም ብቻ ሳይሆን ለመፈፀም ያልቻሉበት ሁኔታ ምንድነው የሚለውን በዋናነት በማየት አሳማኝነቱ ተመዝኖ የቅጣቱ ክብደትና ማነስ እንደሚታወቅም አክለዋል - የህግ ባለሙያው፡፡

Published in ዜና

                   ለቁጥሩ መቀነስ በተሰጠው ምክንያት ኮሚሽኑ ይቅርታ ሊጠይቅ ይገባዋል ተብሏል ለመረጃ ፍተሻው 61 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ገንዘብ ወጪ ሆኗል

የአማራ ክልል ህዝብ ብዛት ከሌሎች ክልሎች በተለየ ሁኔታ ከትንበያው በጣም ዝቅ ብሎ በመገኘቱ የኢንተርሴንሳል ሥነ ህዝብ ናሙና ጥናትና የመረጃ ፍተሻ ተካሄደ፡፡ በጥናቱ ውጤት መሠረትም በህዝብ ቁጥሩ ላይ መሻሻሎች መታየታቸው ይፋ ሆኗል፡፡ ሪፖርቱ ይፋ ባደረገው የዕድገት ምጣኔ ውጤት ላይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ተቃውሞ አሰምተዋል፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር፣ የትምህርት ሚኒስትርና የህዝብ ቆጠራ ኮሚሽን ሊቀመንበር በሆኑት በአቶ ደመቀ መኮንን የቀረበው ሪፖርት እንደሚያመለክተው፤ የ1999/2000 ሶስተኛው የህዝብና ቤት ቆጠራ ውጤት ህዳር 25ቀን2001 ዓ.ም ይፋ ሲደረግ፣ የአማራ ክልል ህዝብ ብዛት ከሌሎች ክልሎች በተለየ ሁኔታ ከትንበያው በጣም ዝቅ ማለቱ በህብረተሰቡ ዘንድ ጥያቄን አስነስቷል፡፡

በዚህ ምክንያትም ተጨማሪ ፍተሻ እንዲደረግ ተወስኗል፡፡ የህዝብ ቆጠራ ኮሚሽን ጽ/ቤት በሰኔ2001 ዓ.ም ለምክር ቤቱ ሪፖርት በቀረበበት ወቅት ምክር ቤቱ የኢንተርሴንሳል ጥናት እንዲካሄድ የወሰነ ሲሆን፡፡ በዚህ መሠረትም ከመንግስት ካዝና በ2004 በጀት ዓመት ብር 64.416.182 ብር፣ ከተባበሩት መንግስታት የሥነህዝብ ፈንድ ደግሞ 9.116.555.34 ብር በአጠቃላይ ብር 73.532.737.34 ተመደበ፡፡ ከዚሁ ገንዘብ ውስጥም 60.837.254.12 ብር ወጪ ተደርጎ የኢንተርሴንሳል ጥናቱና የመረጃ ፍተሻው ተካሄደ ሲሆን ውጤቱም ይፋ ሆኗል፡፡ የቀረበውን ሪፖርት ያደመጠው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፤ በጉዳዩ ላይ ሰፋ ያሉ ማብራሪያ የሚሹ ጥያቄዎችን አቅርቧል፡፡

የቀድሞው ሪፖርት ለምክር ቤቱ በቀረበበት ወቅት፣ የአማራ ክልል ህዝብ ከትንበያው እጅግ ዝቅ ለማለቱ ምክንያት ነው ተብሎ የቀረበው ኤችአይቪ ኤድስ በከፍተኛ ሁኔታ የክልሉን ህዝቦች ማጥቃቱ መሆኑ የተገለፀው አግባብነት የሌለውና የክልሉን ህዝብ ስሜት የነካ በመሆኑ ኃላፊዎቹ እንደ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሥራ ኃላፊዎች፣ ህዝቡን በይፋ ይቅርታ ሊጠይቁ ይገባል የሚል አስተያየት ከምክር ቤት አባላት ተሰንዝሯል፡፡ የክልሉ ህዝብ የዕድገት ምጣኔ እንደሆነ ተገልፆ በቀረበው ሪፖርት ላይም አባላቱ ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡ የህዝቡ አመታዊ የዕድገት ምጣኔ ከ1.73 ወደ 2.3 እንዲያድግ የተደረገ ቢሆንም አሁንም ይህ ቁጥር እንኳንስ በለጋ ዕድሜ ጋብቻን ፈጽሞ በርካታ ልጆች በሚወለዱበት በአማራው ክልል ይቅርና አደጉ በሚባሉ አገራትም ሊሆንና ሊታሰብ የማይችል ጉዳይ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡

እንደ አውሮፓ ባሉ ታላላቅ የአለማችን አገራት ውስጥ የሌለ የዕድገት ምጣኔ አምጥቶ በአማራው ክልል ላይ መደፍደፍ አግባብነት ያለው ተግባር ነው ብለን አናምንም ሲሉም አባላቱ ቅሬታቸውን አቅርበዋል፡፡ በምክር ቤቱ የሚገኙት ብቸኛው የተቃዋሚ ፓርቲ (የመድረክ) ተወካዩ አቶ ግርማ ሰይፉ በበኩላቸው፤ 2.99 ሚሊዮን በሚለው የአዲስ አበባ ህዝብ ብዛትና 2.1 በመቶ የዕድገት ምጣኔው ላይ ቅሬታቸውን ለምክር ቤቱ አሰምተዋል፡፡ በምክር ቤት አባላቱ ለቀረቡት ቅሬታዎችና ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር፤ የትምህርት ሚኒስትርና የህዝብ ቆጠራ ኮሚሽን ሰብሳቢው አቶ ደመቀ መኮንን፤ የቀድሞ ሪፖርት በድጋሚ እንዲታይና የመረጃ ማጣሪያ እንዲደረግ በተሰጠው ውሣኔ መሠረት ማጣሪያው ተሠርቶ ውጤቱ ይፋ መደረጉን ገልፀው፤ ይህ መረጃ በጥቅም ላይ መዋል እንደሚገባው ተናግረዋል፡፡

የማዕከላዊ ስታስቲክስ ኤጀንሲ ስራ አስፈፃሚ ወ/ሮ ሳሚያ ዘካሪያ በበኩላቸው፤ የቀድሞው ሪፖርት ስህተት የነበረው ከትንበያው ላይ መሆኑን ጠቁመው የኢንተርሴንሳል ጥናቱና በመረጃ ማጣራት ሥራው የተገኘው ውጤት ይፋ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ በዚህ መሠረትም በ2004 ዓ.ም በተደረገው የኢንተርሴንሳል ጥናትና የመረጃ ማጣራት ሂደትም የአማራ ክልል ህዝብ ብዛት 19.2 ሚሊዮን መድረሱን እንዲሁም የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ ህዝብ ብዛትም 2.99 ሚሊዮን መሆኑን ጨምረው ገልፀዋል፡፡ ምክር ቤቱ በኮሚሽኑ የቀረበውን የ2004 የኢንተርሴንሳል ሥነህዝብ ጥናት እንዲፀድቅ አድርጓል፡፡

Published in ዜና
Page 6 of 17