በሰሜን አሜሪካ ከሚገኘዉ ታዋቂዉ የፊልም ኩባንያ ከ”አባይ ሙቪስ” እና በርካታ ሀገርኛ ሲኒማ በመስራት ላይ የሚገኘዉ እና በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሥራ ላይ የተሰማራዉ ኦክቴት ኮምፒዉተር ቴክኖሎጂ በመተባበር በሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሚያዘጋጀዉን እና የሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የተመሰረተበትን የ30ኛ ዓመት አከባበር ሥነ-ስርዓት ከሰኔ 23 2005 ዓ.ም እስከ ሰኔ 30 2005ዓ.ም በሰሜን አሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ ሜሪላንድ ዉስጥ በርካታ ቁጥር ያላቸዉ ኢትዮጵያዉያን እና ትዉልደ ኢትዮጵያን በሚገኙበትን ይከበራል፡፡በዚህም ዝግጅት ላይ ታዋቂ የሀገርችን አርቲስቶች የሙዚቃ እና የተለያዩ ባህላዊ እሴቶችን የሚያንጸባርቁ ዝግጅቶችን ያቀርባሉ፡፡ በዝግጅቱም ላይ በርካታ ታዋቂ ስፖርተኞች፣ ጋዜጠኞች የፊልም ባለሙያዎች በዝግጅቱ ላይ ይታደማሉ፡፡ ዝግጅቱ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ይተላለፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ብሉ ኦሽንና ናይት ክለብ በመሪ ሲኤምሲ አካባቢ ተከፈተ፡፡ ክለብ ቪ አይ ፒ ሰርቪስ ያለው መስተንግዶ ጋር የሚሰጥ ከ 70 በላይ ለሰራተኞች እድል እንደፈጠረ በተመጣጣኝ አገልግሎት የተለያዩ ባህላዊና የውጪ አገር ምግቦች ያቀርባል በተለይ አርብና ቅዳሜ በዲጄ ሳሚ ይቀርባል፡፡ ብሉ ኦሽን ናይት ክለብ በዘመናዊ የመብራት እና የድምጽ ቴክኖሎጂ የተዋቀረ በውስጥና የውጭ መስተንግዶ በመስጠት ከሌሎች ናይት ክለቦች በተለይ መልኩ አገልግሎት እንደሚሰጥ ሰኔ 15ቀን 2005 ዓ.ም በተመረቀበት ጊዜ ተገልጿል፡፡

በፋሲል አስማማው ተፅፎ በደረጀ ደመቀ የተዘጋጀው “ጀንኖ” የተሰኘ አዲስ ፊልም ዛሬ በሐዋሳ ከተማ እና በሌሎች ክልል ከተሞች ይመረቃል። በጵንኤል ፕሮሞሽንና ማስታወቂያ ድርጅት ፕሮዱዩሰርነትና በታምሩ ብርሃኑ ፕሮዳክሽን የተሠራው ፊልሙ፣ የሮማንቲክ ኮሜዲ ዘውግ ሲኖረው አልጋነሽ ታሪኩ፤እንቁስላሴ ወርቅ አገኘሁ፣ዘነቡ ገሠሠ፣ ደረጀ ደመቀና ተመስገን ታንቱን ጨምሮ ከ60 በላይ ተዋናዮች ተካፍለውበታል፡፡ ፊልሙ በሐዋሳው የሲዳማ ባህል አዳራሽ በሚመረቅበት በዛሬው ዕለት በዲላ፣ በሻሸመኔ እና በነገሌ ቦረና እንደሚመረቅ የፊልሙ ደራሲ ፋሲል አስማማው ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ በቅርቡም በአዲስ አበባ በሚገኙ ሲኒማ ቤቶች ይመረቃል፡፡

Saturday, 29 June 2013 10:38

የፍቅር ሽልማት

ፍቅር ሽልማት የለውም
አንተ ግን ሽልማት አለህ!
እንደ ትንቢት - ተናጋሪ፣ የነገን ዕውቀት አበጀህ!
የእናት ያባት ዕውቀት ማለት፤
የልጅ ሽልማት ውብ ኩራት!!
የራስህ ትምርት ትጋት
የራስህ ትምርት ንጋት
የዛሬህን ጐዶሎ፣በነገ ጥበብህ መሙላት
ይሄ ብቻ ነው ዓለምህ፣ የራስህ ፍቅር ጉልላት!!
(ነ.መ፤ ኢዮብና አሥቴር ለፍቅር የትምህርት ድል)
ሰኔ 21 2005 ዓ.ም

Published in የግጥም ጥግ

ከዛሬ አሥር ዓመት በፊት በሣሉ ብዕረኛ ተፈሪ መኮንን “ግጥም ሞቷል” ሲል በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ መርዶ በማርዳት ቁጣዬ የበረታ እንደነበር አስታውሳለሁ። ከፀሐፊው ጋር የስልክ ሙግት መግጠሜም አልቀረም፡፡ ውሎ ሲያድር ግን የጥበቡን ሰማይ ሳይ ከዋክብት እየነጠፉ፣ ውበት እየጨለመ ሲመጣ ልቤ ደረቴን በስጋት መደብደብ ጀምራ ነበር፡፡ ያ ሥጋትም ስለግጥም ይበልጥ ማሰብ፣ ከዚያም አለፍ ሲል እያነበቡ ሃሳብ ወደማቅረብ የገፋኝ ይመስለኛል እንደተፈራው፡፡ የግጥሙ ሰፈር ልክ የሌላቸው ገለባዎች መፈንጫም መሆኑ አልቀረም፡፡ ነፍስ የሌላቸው ገለባዎች እንደፈርጥ የሚንቦገቦጉትን የብዕር ውበቶች እንዳያንቁ ብዙዎቻችን ሠግተናል። አዝነን አንገታችንንም ደፍተናል፡፡ ግና አሁን አሁን ሰማዩን ሳየው ተስፋ ያረገዘ፣ ውበት ያነገተ ይመስላል፤ ብዙ ገላባዎች ቢኖሩም ፍሬ ያላቸው ወጣት ገጣሚያን መጋረጃውን ገልጠው ብቅ ብቅ እያሉ ነው፡፡

ወጣትነት ሙሉነት የሚጠበቅበት ዕድሜ አይደለም፡፡ ወደ ሙሉነት የመድረሻ ጉዞ ፍንጭ እንጂ፡፡ የቀደሙትና ብርቱ የሚባሉት ገጣሚያንም መንገድ ከዚህ የተለየ አልነበረም፡፡ አሁን የዘመናችን ወጣት ገጣሚያን መንገድ ጥሩ ተስፋ እየሰጠ ነው፡፡ በጣት የሚቆጠሩ ቢሆኑም ለጥበቡ ውበት፣ መሥመር እያበጁ፣ ሕይወት እያፈሩ መምጣታቸው አይቀሬ ነውና ልብ የሚሞላ ጉጉት ፈጥሯል፡፡ እውነት ለመናገር የቀደመው ዘመን አፍርቷል ከምንላቸው ገጣሚያን የማያንሱ ገጣሚያን ቁጥርም እየፈጠርን ይመስለኛል፡፡ አሁን የሚያስፈልገን የንባብ ባህል ይበልጥ እንዲጨምር በማድረግ እምቡጦቹ አብበውና አፍርተው፣ ጐደሎዎቻችንን እንዲሞሉ ማስቻል ነው፡፡ በቅርብ ጊዜ የታተሙ የግጥም መጻሕፍትን ሳይ የተሰማኝ ስሜት ያ ነው፡፡ ተስፋ ያንለጠለጠለ በሣቅ የታጀበ፡፡ ዛሬ ያየነው ተስፋ ነገ በውበት የደመቁ ዓመታት እንደሚወልዱልን አያጠራጥርም፡፡

ቀደም ሲል በዮሐንስ ሞላ መጽሐፍ ላይ የደመቀ ተስፋ እንዳየሁ ሁሉ የወሎው ገጣሚ መንግስቱ ዘገየም ደስ በሚል ልብና ኃይል ተገልጦ አይቼዋለሁ፡፡ ጋዜጠኛ በረከት በላይነህም “የመንፈስ ከፍታ” በሚለው ጥራዙ የፋርስ ግጥሞችን መርጦ በመተርጐምና የራሱን ግጥሞች በማቅረብ የጥበብ ሆዳችንን ረሃብ ለማስታገስ የሚችል አበርክቶት አኑረዋል፡፡ ደስ ይላል፡፡ የበረከት ግጥሞችን በጥልቀት የመገምገምና የመተንተኑን ሥራ ላቆየውና ለጊዜው ቀልቤን የኮረኮሩትን ግጥሞች ልዳስስ መርጫለሁ፡፡ “የፈሪዎቹ ጥግ” ስሜቴን ከዳሳሱት፣ ሃሳቤን ከነጠቁት ግጥሞቹ አንዱ ነው፡፡ እንዲህ ይነበባል:- በማያውቀው ስንዝር ዕድሜው እንዳይለካ፤ ባልቀመሰው እርሾ ነገው እንዳይቦካ፤ ይፈራል የሰው ልጅ፤ ይሰጋል የሰው ልጅ አይጨብጥ አይነካ፡፡ አይገርምም! መሸጥ አያሰጋው፣ መግዛት እየፈራ፣ “አለመወሰኑን” ትርፍ ብሎ ጠራ፡፡ እኔ የምለው! ቀኝ ግራ ኋላ፣ ፊት - እስካልተከለለ፤ በጥግ - የለሽ ነገር መሃል መስፈር አለ? ይህ ምስኪን ወገኔ! ላበጀው ጥያቄ እስካልተፈተሸ፤ ቅዠት አቅፎ ያድራል - ሕልሙን እየሸሸ፡፡ ገጣሚው በረከት ተናግሮታል ብዬ የማደምቀው ሃሳብ፣ ሰው ነገር የሚያይበት ተጨባጭ ራዕይ፣ የሚጓዝበትን መንገድ የሚያስተውልበት አይን አጥቶ፣ በሰከረ ዓይን የሚዋዥቅ ሆኗል የሚለውን ይመስላል፡፡ ሁሉ አማረሽ በመሆኑ ወደፊት ፈቅ የሚልበትን ምርጫ እንደ ጨርቅ አውልቆ ጥሏል።

መላ ቅጡ በጠፋ ስካር ውስጥ ተዘፍቆ ትክክለኛ አድራሻውን የሚያሳየውን ሕልሙን ወደ ኋላ ዘንግቷል ነው የሚለው፡፡ ሕልም የሌለውና ሕልሙን የሸሸ ሰው መድረሻው የት እንደሚሆን ሊሰብከን አልሞከረም፡፡ የወደደ ሰው ወደ መጽሐፍ ቅዱሱ ዮሴፍ፣ ወዲህ ቀረብ ሲል ደግሞ ወደ ማርቲን ሉተር ኪንግ ተጠግቶ “ሕልም አለኝ” የምትለውን ሃሳብ መፈልፈል አለበት፡፡ ለዚያም መሰለኝ “ይህ ምስኪን” ብሎ ለሕልም አልባው ሰው ከንፈር የመጠጠለት! “ሸማኔ ሲፎርሽ” ለኔ ከተመቹኝ ግጥሞች አንዱ ነው፡፡ “ታታሪው” ሸማኔ! ከመመሳሰል ውስጥ ውበትን ቀምሮ፤ “ጥበብ” ያለብስናል ካንድ ቀለም ነክሮ፡፡ ለባሾች አይደለን? እንተያያለን፤ እንተያያለን፤ ኤዲያ!! ጥለቱ ጋ ስንደርስ እንለያያለን፡፡ መቼም አይታክተን! እንወርዳለን ቆላ፤ እንወጣለን ደጋ፤ ጥለት አመሳሳይ ሸማኔ ፍለጋ እዚህ ግጥም ውስጥ ዋነኛው ተዋናይ ሸማኔ ነው፡፡ በእማሬያዊ ፍቺው ምናልባት ሸማኔው ብዙ ሲሆን፤ በብዙ ሊተነተን ይቻላል፡፡

በርግጥም ስለግጥም የፃፉ ምሁራን እንደሚሉት ግጥም ራቁቱን የተሰጣ ባይሆን ይመረጣል፡፡ ለአንባቢው አዲስ ቃና፣ ፍልፍል ውበት ቢያበቅል ደስ ይላል፡፡ እንደግጥሙ ሆኖልን ጥለት ውበት በመሆኑ ሸማኔ ፍለጋ ላይ ታች ካልን ይገርማል፡፡ ደስ የማይለው ግን ለማመሳሰል መሆኑ ነው፡፡ ከመመሳሰል መለያየት ሳይሻል አይቀርም፡፡ እንኳን ጥበብ ሰው ራሱ ቢመሳሰል ሕይወት ትሠለቻለች፤ ተስፋ ትርቃለች። ቀለምም አያምርም፡፡ ዜማም ይጠነዛል፡፡ በረከት ያለው የትኛው መመሳሰል እንደሆነ ስላላወቅን የየራሳችንን መጠርጠር እንጂ የየልባችንን መደምደሚያ ቀዳዳ የለንም፡፡ ቢሆንም እንዲህ ወዲያ ወዲህ መባዘንም ጥሩ ነው፡፡ መመርመር ክፋት የለውም፡፡ የበረከት “የመንፈስ ከፍታ” የፋርሶቹን ግጥሞችም ይዟል፡፡ ለዛሬ ላስቃኛችሁ የወደድኩት ግን የራሱን የበረከትን ስለሆነ አልነካውም እንጂ እጅግ ያደነቅሁለት ምርጥ ግጥሞችን አስሶ መተርጐሙ ነው፡፡ አሁን ግን ወደ በረከት “ልዩነት” ተመልሼ በመሄድ ጥቂት እላለሁ፡፡

ብዙዎች አንደበቱ ባይጥም፤ ለጆሮ ባይመች ትምህርት አሰጣጡ “ኤዲያ” የጋን ውስጥ መብራት በማለት አድመው ካዳራሹ ወጡ፡፡ ጥቂቶች የመምህሩ ዕውቀት፤ “የጋን ውስጥ መብራት” መሆኑን ያመኑ፤ አምነው የተግባቡ አዳራሹን ትተው “ወደ ጋኑ” ገቡ፡፡ እዚህ ግጥም ውስጥ አንድ መምህር ጐልቶ ይታያል፤ ማስረዳት የማይችል፤ ለሌሎች ዕውቀቱን ማካፈል ያልታደለ፡፡ ቅላፄው ለጆሮ የማይጥም። በዚህ ምክንያት የክፍሉ ተማሪዎች ለሁለት ተከፍለዋል፡፡ አንዱ ወገን እዚህ ሰውዬ ዘንድ ተቀምጦ ጊዜ ከማቃጠል አዳራሹን ለቅቆ መሄድ ይሻላል በሚል መምህሩን ንቆ ትቶት ወጥቷል፡፡ ሌላኛው ወገን ደግሞ መምህሩ ቀሽም በመሆኑ ተስማምቷል፤ ሃሳቡን ለሌሎች ማካፈል የማይችል የጋን ውስጥ መብራት በሚለው ተግባብቷል፤ ስለዚህም በተመሳሳይ አዳራሹን ትተው ወጥተዋል። ግን የውስጡን እሣትና ብርሃን ፍለጋ ጋኑን መፈልፈል ይዘዋል፡፡ የጋኑን መብራት ያነቀው ምንድነው የሚል ፍለጋ ይመስላል፡፡

ተስፋ የቆረጠና ተስፋውን ያልጣለ ወገን ለየቅል ቆመዋል፡፡ መምህሩ የተደበቀ ሕይወት፣ መንገድ ያጣ ውበት ቋጥሯል። ግን መንገድ የለውም፤ ጋን ውስጥ ገብቶ ከጋን ውስጥ እሣቱን ማውጣት ይቻል ይሆን…ቢሆንም የበረከት ከፊል ገፀ ባህርያት ወደ ጋኑ ገብተዋል። አዳራሹ ውስጥ መምህሩ ሻማ መሆን ካልቻለ መምህሩ ውስጥ ያለውን ሻማ ፍለጋ መዳከር ሊጀምሩ ይሆን? ማን ያውቃል? “ኑሮና ጣዕም” ሌላው የበረከት በረከት ነው፡፡ ሙያዬን ታውቃለህ፤ ማጀቴን ታያለህ፤ “እንጀራሽ እንክርዳድ፣ ገበታሽ ጣዕም - አልባ” ለምን ትለኛለህ በል ዝም ብለህ ብላ ቸርቻሪ መንግስታት፣ ሰነፍ ገበሬዎች፤ በዝባዥ ነጋዴዎች፣ በበዙባት ዓለም፤ ጠንካራ ጥርስ እንጂ ቀማሽ ምላስ የለም ሕይወትን አትመራመር፣ አታጣጥም…ዓለም በስግብግቦች ተሞልታለች፡፡

ቀልብ ያለው የለም፤ የሰው ጆሮ ሣንቲም ሲያቃጭል ከመደንበር ያለፈ ማጣጣም አቅቶታል ስለዚህ አቃቂር ለማውጣት አትሞክር! ይልቅ እዚህ ውበት ስትፈለፍል፤ ቃና ስታጣጥም ከሩጫው እንዳትቀር ዓለም ውበቷን ጥላለች፡፡ ሰውየው ብቻህን አትበድ…!ሁሉም ነገር ተናካሽ ጥርስ እንጂ አጣጣሚ ምላስ አጥፍቷል፡፡ ሰውየው አትጃጃል ባይ ትመስላለች፡፡ ጠቅለል ሲል በረከት፤ በቃላቱ ሃይል አያስደነግጥም፤ በዜማ ሽባነት ግራ አያገባም፡፡ ቀለል አድርጐ ስንኝ መቋጠር ይችላል፡፡ ግጥም ቀዳሚ ተግባሩ ደስታ መፈንጠቅ ነው - የሚለውን የበርካታ ምሁራን ሃሳብ ይዞ የሚቀጥል ይመስላል። ወደፊት ደግሞ የተሻለ ችቦ ከመንገዱ ሲንቦገቦግ ይታየኛል፡፡ ተስፋው ሩቅ፣ ዕድሜው ለጋ ነው….የወጣትነቱ እፍታ ጥሩ ነው፡፡ የፋርስ ግጥሞቹ ምርጫና ስልት ደግሞ ልዩ ነው፡፡

Published in ጥበብ

(N.B The Issue “Art for Arts sake” arises when the Individual` is at odds with society) “በፈጣሪ የተሰራን፣ ነገር ግን ያልተሳካን፣ ብልሹ ንድፎቹ ነን” ይላል ፖስት ኢምፕሬሽኒስቱ ቫንጐ፡፡ ይቀጥልናም “አበላሽቶ ስለነደፈን ግን ልንፈርድበት አይገባም” ይህ አባባሉ፤ ለእኔ ፍለጋ መልስ መሆን ቢኖርበትም፤ ከመልስ ይልቅ ጥያቄ የሚያበጅ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ጥያቄው ወይንም ጥያቄዎቹ ጥበብን ለምን እንፈጥራለን? የሚለውን የከረመ ጥያቄ በድጋሚ የሚያጠነክሩ ናቸው፡፡ ለምንድነው የምንፈጥረው? ከተባለ፤ ብልሹውን ንድፍ ለማደስ ነው፤ በአጭሩ፡፡ …በአጭሩ በተሰጠው መልስ ላይ ግን ረጃጅም ጥያቄዎች ይፈለፈላሉ፡፡ እስቲ ጥያቄዎቹን አብረን እንታቀፋቸው፡፡ ውበትን ለውበትነቱ ወይንም ለእውነትነቱ… አሊያም ለሚሰጠን የህይወት አገልግሎት ስንል እንፈጥረዋለን፡፡ አያከራክረንም፡፡

ከፈጠርነው በኋላስ?... የእግዜርን የተበላሸ ንድፍ ለማሻሻል ብለን የሰራነው የአርትኦት ንድፍ የተበላሸ አለመሆኑን ወይንም ቢሆን እንዴት ነው የምናውቀው? …ውበት ማለት ፍፁምነት ከሆነ፤ የፍፁምነት አቅጣጫ ወደ ሰማይ ነው? ወይንስ ወደ ምድር? ለእግራችን ጫማ የሰራልን እና ከጋሬጣ እና ከእንቅፋት የገላገለን ነው አርቲስታችን? ወይንስ ከህይወት እና ከሰው ተፈጥሮአዊ ማንነታችን በምናብ አንሳፎ ሰማይ የከተተንን ነው ፈጣሪ ብለን የምንጠራው? ሰው ወደ ሰው ነው የሚቀርበው ወይንስ ወደ የሰማዩ ፈጣሪ? …ወደ ፈጣሪ ካላችሁስ በየትኛው የተፈጥሮ ክፍሉ? …በስጋ እና አካሉ ወይንስ በሀሳብ እና በመንፈሱ? ለመንፈስ ጫማ ከሚሰራው ጠቢብ… እግር እና መሬቱን በጫማ ከሚያስማማው በምን እንደበለጠ እንዴት እናውቃለን? አርቲስቱ ቄስ ነው? ከሆነ ሰውን ወደ ሰው ነው ወይንስ ወደ ፈጣሪ የሚያቀርበው? Is he the ventriloquist of God; or the ventriloquist of his follow humans? ወይንስ ለማንም ቄስ አይሆንም… ለራሱም ጭምር? ጥበብ አሁን ካልኩት ወይንም እስካሁን ከምናውቀው የተለየ አላማ አለው? ሊኖረውስ ይገባል?... እነዚህ ጥያቄዎችን ለመመለስ ሳንሞክር፣ የጥበብ የውበትን ሚዛን ልንለካ… የለካንበትንም ምክኒያት ልናውቀው አንችልም፡፡

“ቅድመ ሥነ-ውበት” ብለን ልንጠራቸው የምንገደድ ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ጥያቄዎቹን ሳንመልስ የውበትን ደረጃ ማውጣት ባንችልም፤ በየዕለቱ ግን… የተለያዩ ፈጠራዎችን መዝነን አፋዊ ወይንም ፅሁፋዊ ሂስ እንሰጣለን፡፡ የእንትና ግጥም ምርጥ ነው፣ የእንቶኔ ሙዚቃ ትንፋሽ ያሳጥራል… ወዘተ እንባባላለን፡፡ እንዴት ለካነው?፤ እንዴት ነካን… የቱ ጋ? …የበለጠ እንዲነካን ምን መጨመር ነበረበት? መንካት መቻሉ ውበት መሆኑን አረጋጋጭ ነው? ማነው መቶ ፐርሰንት ውበትን የጨበጠ አርቲስት? ወይንም ስንት ናቸው? ለምን መቶ ፐርሰንት ብቻ ጣራው ሆነ… አንድ ሺ ፐርሰንት እንዳይሆን ማን ያዘው? እድሜአችን?… ሰውኛ መጠን? በተመጠነ መጠናችን ውስጥ መጠን የለሹን እንዴት አወቅነው? እግዜር ጥበበኛ ሆኖ እኛን ከሆነ የፈጠረን፤ እኛ መበላሸታችንን ያወቅነው ከምን አንፃር ነው? እኛ የፈጠርናቸው ድርሰቶች ከእኛ ከፈጣሪዎቻቸው አንፃር ራሳቸውን ተመልክተው ተበላሽተናል ይሉ ይሆን?... ከነዚህ ሁሉ ጥያቄዎች አንፃር ውበት የቱ ጋ ነው የሚገኘው?

                                                      * * *

እንደ ጀርመናዊው ሃሳባዊ ሄግል እይታ (Preromonology) ማህበረሰብ ሲስማማ፤ ወይንም ባልተቃረነ ማህበረሰብ ውስጥ ጥበብ አይፈጠርም ይላል፡፡ “Beauty will be lived no longer imagined” ተፈጥሮ እና እውነታ በማህበረሰቡ አእምሮ ውስጥ እና ጋር ግጭት ስለሌላቸው እንቆቅልሽን አይፈጥሩም፡፡ የተፈታ እንቆቅልሽ አዲስ ፍቺ አይፈልግም፡፡ የማህበረሰቡ ትዝታ፣ ህመም፣ አላማ፣ እና ራዕይ አንድ ስለሚሆን ቅራኔ አይኖርም፡፡ ውበቱም፣ እውነቱም አንድ ይሆናል፡፡ ስለዚህ ፈጠራ እና ጥበብ አይኖርም፡፡ የፈጠራ እና የጥበብ አለመኖር አመልካች የሆነው አንድን ነገር ነው፡፡ ግለሰብ የሚባል የተነጠለ ህዋስ መጥፋቱን። ግለሰብ ሲኖር፤ ከማህበረሰቡ ጋር ለመቀላቀል፣ አሊያም ማህበረሰቡን ወደ እሱ ማንነት ለመቀየር ቅራኔ ይፈጥራል፡፡ ጥበብ የቅራኔው መገለጫ ነው። ቅራኔው እንቆቅልሽ ተብሎ ይጠራል፡፡ በግለሰብ እና በማህበረሰብ መሀል የሰማይ እና የምድር ያህል ልዩነት አለ፡፡ በእኔ እይታ፣ መሬት እና ሰማይ ማህበረሰብን እና ግለሰብን ለመግለፅ የምንጠቀምባቸው ልኮች ናቸው፡፡ ብዛትን ገላጭ ናቸው፡፡ ውበትን ወይንም እውነትን ሳይሆን የቁጥር ብዛትን ይወክላሉ። በብዛት ያነሰው ሰማይ ነው፡፡ ከሼክስፒር እና ከጫማ ጠጋኙ ማነው በቁጥር ብዛት የሚበልጥ ካላችሁኝ መልሱ፤ ጫማ ጠጋኙ ነው፡፡ ጫማ ጠጋኙ መሬት ነው፡፡

ሼክስፒር ሰማይ ነው፡፡ (ሰማይ ስል ከፍታ፣ እግዜር፣ ምርጥ፣ ብርሃን፣ መንግስተ ሰማይ … ወዘተ የሚሉትን ባህሪ ገላጭ እይታዎችን ወደ ጐን እንድታደርጉ በትህትና እጠይቃለሁ) ሼክስፒር ጥቂት (አሊያም አንድ) ጫማ ጠጋኙ ብዙ ነው፡፡ ፒሳሬቭ የሚባል የሩሲያ አልቦአዊ (nihilist) “I would rather be a Russian shoemaker than a Russian Raphel” ይላል። ጫማ የሚሰራልኝን እንጂ የማልገለገልበትን ውበት የሚጠበብብኝ አርቲስት (እንደ ራፋኤል) አያስፈልገኝም ማለቱ ነው፡፡ ወደ ምድር ነው። ወደ ሰው ልጅ፡፡ የሰው ልጅን አካል ከብርድ ከከለልን እና የማህበረሰቡን እግር በጫማ ከሸፈንን ለመንፈስ ብርድ አንጨነቅ፤ ሰው መሆናችንን አንድ ላይ ካመንን ውበቱ ይኸው ነው፤ እንደማለት ነው፡፡ ለምድር፤ የሰማይ ጥበብ አያስፈልግም፡፡ ምድርን በመሰለ ቁጥር ውበትና እውነት ነው፡፡ በቂው ነው። ከዚህ በተቃራኒ፤ ግለሰብነት በበዛበት አለም ደግሞ ሼክስፒር ይፈለጋል፤ ውበት ነው፡፡

ጫማ ሰሪው ከሚገንንበት አለም የግለሰቡ ሃሳብ ከሚቆለጳጰስበት አለም የራቀ ነው፡፡ የሼክስፒር “ሰማይ የሚወደስበት እና የጫማ ሰሪው ምድር የምትወደስበት ዘመኖችም የተለያዩ ናቸው፡፡ ኒቼ (In “the birth of tragedy…”) ምድር እና ሰማይን ለማቀላቀል ሞክሮ ነበር፡፡ ምድር እና ሰማይን ለማቀላቀል በሁለት አፍ ማውራት አስፈልጐት ነበር፡፡ አንደኛው አፍ ወደ “Dionysian ሌላኛው ወደ Apollonian” አፖሎናዊ:- ወደ ግለሰብ የሚያደላ፣ በግለሰብነቱ ምክኒያት ወደ ሰው ልጅ ከሚቀርበው ይልቅ ወደ እውቀት፣ መንፈስ ከፍታ የራቀ…. ፍፁምነት ወደ ሰው በመቅረብ ሳይሆን ወደ እውቀት፣ እና የሀሳብ መራቀቅ አስጠግቶ፣ አካልን ረስቶ ለመንፈስ እና የጭንቅላት አቅም የሚያደላ አድርጐ ይገልፀዋል፡፡ “አይዲያሊዝም” ልንለው እንችላለን፡፡ ዳይኖኤዥያን:- ምድራዊ፣ ለእንስሳ አለም የወሲብ እና ጭካኔ ተፈጥሮው የቀረበ፣ እውነታ በግለሰብ አእምሮ ሳይሆን በማህበረሰብ የሚፈታ በተፈጥሮ ትስስር እና አንድነት (Primordial Unity) የሚገለፅ መሆኑን የሚያምኑ ናቸው፡፡

በእግር ኳስ ሜዳ ወይንም በዘፈን ጭፈራ አንድ ሆነው የሚሰባሰቡ “In which everyone feels himself not only united, reconciled, and fused with his neighbor, but as one with him” (እዚህ ጋር ራሴ እምነት እንድደፍር ይፈቀድልኝ፡- የእግር ኳስ ውጤታችን ጥሩ እንዲሆን፤ የግጥም ውጤታችን አፈር ድሜ መብላት አለበት) በእዚህ ሁለትዮሽ ድብልቅ (እንደ ኒቼ አገላለፅ) የሰው ልጅ በአካሉ (ማህበረሰብ) እና በግለሰቡ (ሀሳቡ) መሀል ሳይበጠስ አንድ ላይ ተሳስሮ ማስቀመጥ ይቻላል፤ ባይ ነው፡፡ በኒቼ እምነት ዳይኖስየስን (ማህበረሰብን) የገደለው አፖሎ (አይዲያሊዝም) መሆኑ ነው፡፡ ምድርን የገደለው ሰማይ ነው በአጭሩ፡፡ ይሄንን ነጥብ ይዘን የቅድሞቹን ጥያቄዎች ተመልሰን እንያቸው፡፡ ቫንጐ የፈጣሪ ብልሹ ንድፎች ነን ማለቱ፤ ፈጣሪን ፍፁም አድርጐ መቀበሉን አመልካች ነው፡፡ ወደ ሰማይ፣ ወደ ሀሳቡ… ወደ ግለሰብ ምልከታው የሚያደላ ነው፡፡ ከማህበረሰቡ ጋር ቅራኔ ውስጥ ያለ ነው፡፡ ሀሳቡ በአካሉ ውስጥ እስረኛ ሆኖ ምድር እንዲርቀው ሆኗል፡፡ በቀደመ (የተነጠለ) ሀሳቡ የሰራቸው በቁጥር ወደ ሁለት ሺ ገደማ ብዛት ያላቸው ስዕሎቹ በህይወት በነበረበት ወቅት ተሸጠውለት አያውቁም፡፡

ማህበረሰቡ በቁጥር ብዙ ነው፡፡ እንደ ጫማ ሰፊው ለወቅታዊ አገልግሎቱ የሚሆን መፍትሄ የሚሰጠው አርቲስት ይሻል፡፡ ቫንጐ ማህበረሰቡን መራቅ የቻለው፤ ከሰው በላይ በጋለ ስሜታዊነቱ፣ በጥበቡ፣ በእብደት እና በሞት ብቻ ነበር፡፡ ለሰማይ ዘልሎ ጣራ ነክቶ ተመለሰ፡፡ መሬት ላይ የሚኖሩ ስዕሉን ከሞተ በኋላ ተረዱለት፡፡ በሞተበት ገዙት፡፡ ግለሰቡ አርቲስት “ሰው የፈጣሪ የተበላሸ ንድፍ ነው” እንዳለው፡፡ ማህበራዊ አርቲስቱ “ለማህበረሰቡ አስተዋፅኦ የማያደርግ ሀሳብ ፀረ-ህዝብ” ነው የሚል ይመስለኛል፡፡ ከቫንጐ ይበልጥ ዳቦ ጋጋሪው ለማህበረሰቡ ይጠቅማል፡፡ ዳቦ ጋጋሪው ሼክስፒር ይሆንለታል፡፡ እንግዲህ፤ መሬት እና ሰማይ ይህንን ያህል ቢለያዩም፣ ሁለቱም በሰው አማካኝነት እየተፈራረቁ እስከምናውቀው የአሁኑ ዘመን ዘልቀዋል፡፡

ውበትን ለመመዘን መሬቱም - አየሩም - ሰማዩም ያስፈልጉናል thesis, antitheisis and synthesis ሺፑትሊን (A.P. SHEPTULIN) የተባለ የማርክሲስት ሌኒኒስት ፈላስፋ ማቆራኘት እና መነጣጠል የተለያዩ ሳይሆኑ አንድ ነገር እንደሆኑ ይገልፅልናል Although connection and isolation are different types of relations, they exist together, in union, rather than separately. The existence of connection involves the existence of isolation and vice versa መሬት የሚሰጠው ምርት ከመልከአ ምድራዊ አቀማመጡ ጋር ቁርኝት አለው፡፡ ሁለቱ የተነጣጠሉ ቢመስሉም ግንኙነት አላቸው፡፡

መሬቱ እና የአየር ፀባዩም ግንኙነት አላቸው፡፡ …በዚሁ አተያይ ለዘመናችን ጥበብ ማበብ ወይንም መድረቅ የአየሩ ሁኔታ አስተዋፅኦ አለው፡፡ የፖለቲካው የአየር ሁኔታ፡፡ መሬት እና ሰማይም በመነጣጠላቸው ውስጥ አንድነት ሁሌም ይኖራቸዋል፡፡ የመሬት ሰብል ለመሬት እንጂ ለሰማይ አይጠቅምም፡፡ የሰማዩም ለመሬት እንደዚሁ፡፡ በመግቢያ ላይ የጠየቅኋዋቸው የጥበብ/ውበት መለኪያ ጥያቄዎችም እንደ አየሩ ሁኔታ እና እንደ መልከአ ምድሩ አቀማመጥ መልሶቻቸው የሚለያዩ ይሆናሉ፡፡ ነገር ግን በልዩነቱ ውስጥም አንድነት አላቸው፡፡ ሰው በግለሰብነቱ ዘመን የፃፋቸው የምናብ ነክ ሀሰሳዎች፣ ሰው በማህበረሰብነቱ ዘመን ከሚፅፋቸው፣ ከሚዘፍናቸው፣ ከሚቀኛቸው በእጅጉ የተለዩ ናቸው፡፡ የማህበረሰብነት ዘመን ሲመጣ እንደ ምስኪኑ ቫንጐ ከመሆን ያድነን፡፡ ባይሆን እንደ ኒቼ መሬት እና ሰማዩን ቀላቅሎ… መሐል ቤት (አየር) ላይ መንሳፈፍ ሳይሻል አይቀርም፡፡

Published in ጥበብ

እንዲህ እንደዛሬው አገልግሎቱ በአብዛኛው ለተለየ ዓላማና ተግባር እንዲውል ከመደረጉ በፊት የማሣጅ አገልግሎት (ህክምና) በአገራችን የተለመደና አዘውትሮ የሚከናወን ጉዳይ ነበር፡፡ የጥንት የአገራችን ሰዎች ጐንበስ ቀና ሲሉ የዋሉበት ሰውነታቸውን ከቤት ውስጥ ተንጦ በተዘጋጀ ለጋ የከብት ቅቤ በመታሸት እንዲፍታታና ሰውነታቸው ዘና እንዲል ማድረጉ የየዕለት ተግባራቸው ነበር፡፡ ነገስታቱ ሣይቀር የማሳጅ አገልግሎቱን አዘውትረው ይጠቀሙ እንደነበርና ለጦርነትም ሆነ ለተለያዩ ጉዳዮች ከአገር አገር ይዘዋወሩ በነበረበት ጊዜ ሁሉ ይህንኑ አገልግሎት የሚሰጧቸውን ሴቶች (የጭን ገረድ) ይዘው ይንቀሳቀሱ እንደነበር ታሪክ ይነግረናል፡፡

የማሳጅ ህክምና ከ3ሺ ዓመታት በፊት በቻይና የተለመደ ጉዳይ ነበር፡፡ የተሳሰረና አልፍታታ ያለን ጡንቻ፣ ጥበባዊና ሣይንሳዊ በሆነ መንገድ በማሸት እንዲፍታታ የማድረጉን ተግባር ቻይናዎቹ ተክነውበታል፡፡ የማሣጅ ቀጥተኛው ትርጓሜ የተለያዩ የሰውነት ክፍሎችን በእጅ መዳፍ ማሸት የሚለው ሲሆን አስተሻሸቱ ለስላሳና ጠንከር ባለ መንገድ ሆኖ የራሱ ጥበባዊ ዘዴ ያለው ነው፡፡ የማሣጅ ህክምና የተለያዩ ጡንቻዎችንና የመገጣጠሚያ ጅማቶችን በማሻሸት እና ጫን ጫን በማድረግ አካልን ለማፍታታት እንዲሁም ጡንቻና መገጣጠሚያዎችን እንዲፍታቱ ለማድረግ የሚረዳ ዘዴ ነው፡፡ አንዳንድ የማሣጅ አይነቶች ከእጅ በተጨማሪ የተለያዩ መሳሪያዎችንና ሙቀትን ይፈልጋሉ፡፡ ጀርባ፣ ትከሻ፣ አንገት፣ የእግር ጡንቻ፣ ወገብ፣ በማሳጅ የሚዳሰሱ የአካል ክፍሎች ናቸው፡፡

ማሳጅ ከሚያስገኛቸው ጥቅሞች ዋንኛው በጡንቻና በመገጣጠሚያ አካባቢ የደም ዝውውርን ከፍ ማድረግና ከሰውነታችን የሚወጣውን ተረፈ ምርት (ቆሻሻ) በአግባቡ እንዲወገድ ማድረግ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ሰዎች ማሳጅን በተለያዩ ምክንያቶች ይጠቀማሉ፡፡ ዘና ለማለት፣ ከጭንቀት ለመላቀቅ፣ ለስፖርት እንቅስቃሴ ለመዘጋጀት የተሳሰሩ ጡንቻዎችን ለማፍታታት፣ አሁን አሁን ደግሞ የወሲብ ፍላጐትን ለማነሳሳት ማሳጅን ይጠቀማሉ፡፡ የማሳጅ ህክምና በሙያው በሰለጠነ ሰው ካልተከናወነ እጅግ ለከፋ ጉዳትና ለሞት ሊዳረግ እንደሚችል የማሳጅ ቴራፒ ባለሙያው አቶ ዮሐንስ ደረጀ ይናገራል፡፡

ሙያው የራሱ የሆነ ጥበባዊ የአስተሻሸት ዘዴና ቅደም ተከተላዊ አሠራር ያለው በመሆኑ ጥንቃቄ ሊደረግበት የሚገባ መሆኑንም ይገልፃል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከሰባ አምስት በላይ የማሳጅ አይነቶች መኖራቸውን የሚገልፀው የማሳጅ ቴራፒስቱ ዮሐንስ፤ ሁሉም የማሳጅ አይነቶች የየራሳቸው ባህርይና የአስተሻሸት ዘዴ እንዳላቸው ይጠቁማል፡፡ ጥሩ ማሳጅ ፀጥታ በሰፈነበት፣ ብርሃን ባልበዛበት ሥፍራ እንደሚደረግ የሚገልፀው ባለሙያው፤ ሥራው በለስላሳ ሙዚቃ ታጅቦ ለእሽታው የሚያገለግሉ የተለያዩ አይነቶች ቅባቶችን በመጠቀም እንደሚከናወን ይገልፃል፡፡ አገልግሎቱ የሚሰጠውም በሙያው በሰለጠነ ሰው መሆን እንደሚገባውና ይህ ካልሆነ ግን ከአካል ጉዳት እስከሞት ሊያደርስ የሚችል ጉዳት ሊፈጥር እንደሚችል ይናገራል፡፡ በአሁኑ ወቅት በአገራችን በማሳጅ ሙያ ላይ ስልጠናን የሚሰጡ የተለያዩ ድርጅቶች መኖራቸውን የጠቆመው አቶ ዮሐንስ፤ እነዚህ ድርጅቶች ስልጠናውን የሚሰጡት በተገቢው መንገድና በሙያው በቂ ዕውቀት ባላቸው እንዲሁም ሙያውን ሣይንሳዊ በሆነ መንገድ ሊያስተምሩ በሚችሉ ባለሙያዎች ነው ለማለት ግን እንደማያስደፍር ይገልፃል፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአገራችን በተለይም በመዲናችን አዲስ አበባ እጅግ በሚያስገርም ፍጥነት እየተስፋፋ የሚገኘው የማሳጅ አገልግሎት፣ ዛሬ ዛሬ ቀደም ሲል ከነበረው አገልግሎቱና አሠራሩ በተለየ መንገድ መከናወን ጀምሯል፡፡ በከተማዋ የማሳጅ አገልግሎት በሚሰጥባቸው ቤቶች ውስጥ ከመደበኛው የእሽታ አገልግሎት ውጪ ግማሽ ፓኬጅ እና ሙሉ ፓኬጅ በሚል መጠሪያ የሚሰጡት አገልግሎቶች እጅግ አስፈሪና አሳሳቢ እየሆኑ መምጣታቸውን በሴቶች ወጣቶችና ህፃናት ጉዳይ ቢሮ የተደረገውና በቅርቡ ይፋ የሆነው ጥናት ያመለክታል፡፡ ቢሮው በጉዳዩ ላይ በስፋት አደረግሁት ያለው ጥናት እንደሚያመለክተው፤ በከተማው ውስጥ ከሚገኙት የማሳጅ ቤቶች አብዛኛዎቹ ከማሳጅ አገልግሎት በተጨማሪ የወሲብ ገበያ ያደሩበታል፡፡ በማሳጅ ቤቱ ውስጥ አገልግሎቱን ለማግኘት የሚመጡትን ሰዎች የሚያስተናግዱት “ባለሙያዎች” ከእሽታ (ከማሣጅ) ሙያ በተጨማሪ ጥሩ ቁመናና መልክ እንዲኖራቸው ያደርጋል፡፡ አገልግሎቱን ከማሳጅ ቤቱ ውጪ በሆቴል፣ በመኖሪያ ቤትና በመኪናዎች ውስጥ ሁሉ ለማግኘት ለሚፈልጉ ደንበኞችም “ባለሙያዎቹ” እንደየሁኔታው አገልግሎቱን እንዲሰጡ ያደርጋል፡፡

ጥናቱ በዚህ አገልግሎት ተጠቃሚ የሆኑና በተለያዩ ሥፍራዎች ከማሳጅ ቤቶች “ባለሙያዎችን” እየወሰዱ የሚጠቀሙ በርካታ ባለሃብቶች፣ ባለስልጣናትና የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች መኖራቸውንም ጠቁሟል፡፡ የማሳጅ አገልግሎቱ የሚሰጥባቸውም ትላልቅ ህንፃዎች፣ ሰፋ ያለ ግቢ ያላቸው ቤቶች፣ አፓርትማዎችና በከተማዋ ዋና ዋና አካባቢዎች በሚገኙ ፎቆች ላይ የሚገኙ ቤቶች መሆናቸውን አረጋግጧል፡፡ ይህ ሁኔታ የማሳጅ ህክምናን ወደአላስፈላጊ መንገድ እንዲያመራና ህክምናው በተገቢው መንገድ ለተጠቃሚው እንዳይደርስ የሚያደርግ መሆኑ የማይካድ ሃቅ ነው፡፡ ከሰባ አምስት በላይ የማሳጅ አይነቶች መኖራቸውን የሚናገረው የማሳጅ ቴራፒስቱ አቶ ዮሐንስ፤ በአገራችን የተለመዱት ግን እጅግ ጥቂቶቹ ብቻ መሆናቸውን ይገልፃል፡፡ ከእነዚሁ በአገራችን በስፋት ከተለመዱትና በበርካታ የማሳጅ አገልግሎት መስጫ ቤቶች ከሚዘወተሩት መካከል ጥቂቶቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡ ስዊድሽ ማሳጅ ይህ የማሳጅ አይነት በአገራችን በስፋት የሚዘወተር የማሳጅ አይነት ሲሆን አሠራሩም ሰውነት ዘና እንዲል ለማድረግ ቅባትን በመጠቀም ረዘም ላለ ሰዓት ውጫዊ ሰውነትንና ጡንቻዎችን በዝግታ ማሸት ነው፡፡ የማሳጅ ባለሙያው ይህንን አይነት አገልግሎት በሚሰጥበት ወቅት ደንበኛው ሰውነቱም ሆነ መንፈሱ ዘና እንዲል በማድረግ በዝግታ ማከናወን ይጠበቅበታል፡፡

ይህ የእሽታ ሕክምና በአግባቡ ከተደረገ ከብዙ በሽታዎች እፎይታን ለማስገኘትና ሰውነትንና ጡንቻዎችን ለማፍታታት ይረዳል፡፡ አሮማ ቴራፒ ይህ ቴራፒ የሚከናወነው በተለይ ከአዕምሮ ውጥረት ጋር ተያያዥ የሆኑ ችግሮች ላለባቸው ሰዎች ነው፡፡ ጥሩ ሽታ ባላቸው ቅባቶች በመጠቀምና ህመምተኛው ዘና እንዲል በማድረግ የሚከናወን እሽታ ነው፡፡ ይህንንም የማሳጅ ሕክምና በርካታ የማሳጅ ቤቶች ይጠቀሙበታል፡፡ ዲፓቲሹ ማሳጅ ይህ የማሳጅ አይነት ውስጣዊ በሆነው የጡንቻና የመገጣጠሚያ ክፍል ትኩረት አድርጐ የሚከናወን ሲሆን ባለሙያው በዝግታ የጡንቻ አወራረድንና የሰውነት ቅርጽን በመከተል እሽታውን ያከናውናል፡፡ ይህ አይነቱ ማሳጅ ረዘም ላለ ጊዜ የቆየ የጡንቻ ህመምን፣ የሰውነት ቅርጽ መበላሸትና፣ የተወለጋገዱ የሰውነት አካላትን ለማስተካከልና ከጉዳት ለማገገም ይመረጣል፡፡ በአጠቃላይ የማሳጅ ሕክምና ሰውነትን ዘና ለማድረግ፣ የጡንቻ ውጥረትን ለማስወገድ፣ ጥሩ ስሜት ለመፍጠር፣ የሰውነት መሳሳብና መተጣጠፍን ለመጨመር፣ ድብርትንና ጭንቀትን ለማስወገድ፣ የደም ዝውውርን ለማቀላጠፍ፣ የወሲብ ስሜት እንዲጨምር ለማድረግ እንደሚረዳ ባለሙያው አቶ ዮሐንስ ይናገራሉ፡፡

የማሳጅ አገልግሎቱ በተገቢው ባለሙያና በትክክለኛው ቁሳቁሶች እየታገዘ ሊሰጥ ይገባዋል የሚሉት ባለሙያው፤ የመታሻ ወንበርና ጠረጴዛ፣ የመደገፊያ ትራሶች፣ የእግር ማሳረፊያ፣ የአንገት ማንተራሻ፣ ልዩ ልዩ ቅባቶችና የኤሌክትሪክ ጡንቻ ማነቃቂያ መሳሪያዎች እንደሚያስፈልጉትም ይገልፃሉ፡፡ ይህ በሌለበት ሁኔታ ያለ ባለሙያና ትክክለኛ የማሳጅ ህክምና መስጫ መሣሪያ የሚከናወነው ማሳጅ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ የጐላ መሆኑንም ባለሙያው ይናገራሉ፡፡ የማሳጅ ህክምና ለሁሉም ሰው አስፈላጊና ተመራጭ ህክምና መሆኑን የሚገልፁት አቶ ዮሐንስ፤ ህክምውን መጠቀም እንደሌለባቸው የሚመከሩ ሰዎች እንዳሉም ይናገራሉ፡፡ ከእነዚህ መካከልም የደም መጓጐል ችግር ያለባቸው፣ ለቅባቶቹ አለርጂ የሚሆኑ ሰዎች፣ በቀላሉ የሚላላጥ ቆዳ ያላቸው፣ እርጉዞች፣ የአጥንት መሳሳት ችግርና ጠንከር ያለ ውስጣዊ የጤና ችግር ያለባቸው ሰዎች ህክምናውን ባይወስዱ እንደሚሻል ይገልፃሉ፡፡ የማሳጅ ህክምና ለበርካታ በሽታዎች እፎይታንና እረፍትን እንደሚሰጥ ሁሉ በአግባቡ ካልተከናወነም የሚያስከትለው ችግር ከፍተኛ ነውና ጥንቃቄ ሊደረግበት ይገባል ሲሉ ባለሙያው ያሳስባሉ፡፡ በየአካባቢው በሚገኙ ማሳጅ ቤቶች ውስጥ ከሚገኙት ሠራተኞች መካከል ምን ያህሉ ሙያውን የተማሩና ሥራቸውን በአግባቡ የሚያከናውኑ ናቸው የሚለውን ለማወቅ ግን ጥናት ያስፈልጋል፡፡

Published in ዋናው ጤና

እናንተዬ --- ሰሞኑን በኢቴቪ የቀረበውን በአሰላ ከተማ ላይ የሚያጠነጥን ጉደኛ “ፊልም” አይታችሁልኛል - ርዕሱ “የመልካም አስተዳደር ችግሮች” የሚል ነው፡፡ እኔማ እንደ አሪፍ ልብ አንጠልጣይ ፊልም ነው የኮመኮምኩት - አንዴ ሳይሆን ሁለቴ፡፡ ኢቴቪ አይደግመውም እንጂ አሁንም ደግሜ ባየው አልጠግበውም፡፡ (ኢቴቪ በህዝብ ጥያቄ መድገም ተወ እንዴ?) እውነቴን ነው --- ከአንዳንድ የአገራችን ቀሽም ፊልሞች አስር እጅ ያስንቃል እኮ! በእርግጥ ይኼኛውም የአሰራር ቴክኒኩ እንጂ ጭብጡ ቀሽም የመንግስት ሹማምንት ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን ነው፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን በጉጉት የሚታይ ምርጥ የመርማሪ ጋዜጠኝነት ሥራ ነው፡፡

በዚህ አጋጣሚ የኢቴቪ መርማሪ ጋዜጠኞችን ላደንቃቸው እፈልጋለሁ (አንዳንዴ መርማሪ ፖሊስ የሆኑ ቢመስላቸውም!) እውነቴን እኮ ነው --- የአሰላ ከተማ አስተዳደርና የከንቲባ ቢሮውን ገበና አፍረጠረጡት እኮ፡፡ እኔ የምለው--- ኢንተርኔት ከመጣ ወዲህ የሰው ገመና የሚባል ነገር ቀረ አይደለ? የ“ቢግ ብራዘር አፍሪካዋ” ቤቲ ገመናዋ የወጣው እኮ በኢንተርኔት ነው (እሷ የአገር ገፅ ግንባታ ብትለውም!) ኢንተርኔት የአምባገነን መሪዎችንም ገመና አልማረም (እኔን ያላመነ እነ ሆስኒ ሙባረክን ይጠይቅ!) እንግዲህ በኢቴቪ ዘገባ መሰረት፣ የአሰላ ከተማ ከንቲባ ቢሮና ማዘጋጃ ቤት ከፍተኛ የመልካም አስተዳደር ችግሮች እንዳሉባቸው ለመረዳት ተችሏል፡፡ ወዳጆቼ --- የፈፀሙት ጥፋት ቀላል እንዳይመስላችሁ --የመጪውን አመራር ጥፋት ሳይቀር የፈፀሙ ነው የሚመስሏችሁ፡፡ እኔማ ዘገባውን እየተከታተልኩ ሳለሁ ከአሁን አሁን እንደ እግር ኳስ ፌዴሬሽን “ይቅርታ” ሊጠይቁ ነው ብዬ በጉጉት ስጠባበቅ ነበር፡፡

ይቅርታ መጠየቃቸው እንዳማረኝ ቢቀርም ለአሪፍ ድራማ የሚሆን አሪፍ መነሻ ሃሳብ በነፃ ስላገኘሁ አልቆጨኝም፡፡ ይኸውላችሁ --- ሥራ አጥ ወጣቶች ተደራጅተው ሊሰጧቸው ይገቡ ከነበሩ ሱቆች መካከል የሚበዙት ታሽገዋል፡፡ (ለማን ይሆን የታሸጉት?) ይህ በእንዲህ እንዳለ አንዳንድ ባለሃብቶች ደግሞ አራትና አምስት ሱቆች ይዘው እንደሚያከራዩ ኢቴቪ ያነጋገራቸው ነዋሪዎች በምሬት ተናግረዋል (ጦቢያችን ምሬት ብቻ ሆነች እኮ!) ኑሮና የመንግስት ሹማምንቶች መከራዋን ያበሏት የአሰላ ነዋሪ፣ ዓይኖቿ በእንባ እርሰውና በርበሬ መስለው “ባዕድ አገር ብንሰደድ ምን ይጠቀማሉ?” ስትል በምሬት ጠይቃለች - በአገራችን እንዳንሰራ አድልዎ ፈፅመውብናል ያለቻቸውን አመራሮች፡፡ የከተማዋ ሌላ ችግር ደግሞ ምን መሰላችሁ? ባለሃብቶች ለኢንቨስትመንት ብለው የተረከቡትን መሬት እስከ አስር ዓመት ድረስ አጥረው ቢያስቀምጡም ቀጪም ተቆጪም አጥተዋል ተብሏል (ምናልባት በ“እጅ” እየሄዱም ሊሆን ይችላል!) በአዲስ አበባ የሚገኝ አንድ የሃይማኖት ተቋም የፃፈው አስገራሚ ደብዳቤ ምን ይላል መሰላችሁ? “የማዘጋጃ ቤትና የወረዳ ቢሮክራሲውን በቀላሉ ማለፍና ጉዳያችንን ማስጨረስ እንድንችል በእግር ብቻ ሳይሆን በእጅም መሄድ ስለሚያስፈልግ ለዚሁ ተግባር የሚውል 50ሺ ብር ያለ ደረሰኝ ከባንክ እንዲወጣ ---” ሲል ማዘዙን ሰምተናል፡፡

(ሃይማኖትና ሙስና እጅና ጓንት እንዳይሆኑ ሰጋሁ) እቺ አገር እኮ ግርም ትላለች፡፡ ከአምስት ደርዘን በላይ የሙስና ተጠርጣሪዎች ተይዘው በከፍተኛ ምርመራ ላይ ባሉበትና ጠ/ሚኒስትሩ ጉዳዩን በግሌም ጭምር እከታተለዋለሁ ባሉበት በአሁኑ ሰዓት፣አንድ አቃቤ ህግና ፖሊስ “የክስ መዝገብ እናዘጋለን” በሚል አስር ሺ ብር ጉቦ ሲቀበሉ እጅ ከፍንጅ መያዛቸውን ሰሞኑን በኢቴቪ ዜና ሰምተናል (ከዚህ በላይ “ፋታሊስት” መሆን አለ እንዴ?) የአሰላን ነገር አልጨረስኩም እኮ! የኢቴቪው ጋዜጠኛ እንዳልኳችሁ የከተማዋን አስተዳደርና የከንቲባውን ቢሮ ቀውጦት ነው የሰነበተው - ዘገባው መቼ እንደተሰራ ባላውቅም፡፡ መቼም ለአመራሮቹ --- ጋዜጠኛ ሳይሆን “የባለቤቱ ልጅ” ሳይመስላቸው አልቀረም ብዬ ጠርጥሬአለሁ፡፡ እኔ የኢቴቪን ጋዜጠኛ ብሆን ግን ምን እንደማደርግ ታውቃላችሁ? የአስተዳደሩ አመራሮችና ከንቲባው ጭምር እንደ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አመራር ህዝቡን ይቅርታ እንዲጠይቁ አደርጋቸው ነበር - ሥልጣን ማስለቀቁ ቢቀር እንኳን (የግምገማ ጊዜ ለመቆጠብ እኮ ነው) ለምን መሰላችሁ? በጋዜጠኛው ከቀረቡላቸው ጥፋቶች ውስጥ አንዱንም በስህተት እንኳን አላስተባበሉም እኮ! ሁሉንም አምነዋል፡፡

በዚያ ላይ ተበዳዮችም ግጥም አድርገው መስክረውባቸዋል። ስለዚህ በነካ እጄ ይቅርታ ጠይቁ ብላቸው ህግን መጣስ ይሆናል እንዴ? (የፌዴሬሽኑ አመራርም እኮ ይቅርታ የጠየቀው በስፖርት ጋዜጠኞች ፊት ነው!) ከሁሉም ደግሞ አዝናኝና አስገራሚ ምላሽ የሰጡት ከንቲባው ናቸው! በእርግጥ መጀመሪያ ላይ ኮራ፣ ጀነን ለማለት ዳድቷቸው ነበር - ሃላፊነቱን በቅጡ እንደተወጣ ሃላፊ፡፡ እናም --- ለአንዳንድ ጥያቄዎች-- “ማለት?” “ሲባል?” ፣ “አልገባኝም!” የሚሉ በትዕቢት የታጀቡ የሚመስሉ ምላሾችን ሲሰጡ ታይተዋል፡፡ ደግነቱ ብዙም አልዘለቁበትም። ጋዜጠኛው መረጃዎችን እየዘከዘከ ሲያፋጥጣቸው የዋዛ እንዳልሆነ ገባቸው፡፡ (የአራዳ ልጅ ናቸዋ!) እናም ከመቅፅበት የአጨዋወት ስልታቸውን ቀየሩ፡፡ ከመጀነንና ከመኩራራት ወደ መለሳለስና ማግባባት ገቡ፡፡ በነገራችሁ ላይ አብዛኞቹ የመንግስት ሹማምንት ጋዜጠኛ ኢንተርቪው በሚያደርጋቸው ወቅት የአደጋ ቀጠና ውስጥ የገቡ ከመሰላቸው፣ ሸውደው የሚያልፉባት የተለመደች የአነጋገር ስታይል አለቻቸው - ከሸማቾች የህብረት ሥራ ማህበር በራሽን የተከፋፈለች የምትመስል፡፡

ከመደጋገሟ የተነሳ የማያውቃት ያለ አይመስለኝም። ለምሳሌ ጋዜጠኛው “ለምንድነው ታዲያ ችግሩ እስካሁን ያልተፈታው?” ብሎ ይጠይቃቸዋል፡፡ ከንቲባው ሲመልሱ “እየሄድንበት ያለንበት ሁኔታ ነው ያለው” ብለው ቁጭ ይላሉ (ግራ ለማጋባት እኮ ነው!) ቆይ ግን-- “እየሄድንበት ያለንበት ሁኔታ ነው ያለው” ሲባል ምን ማለት ነው? ችግሩን እየፈታን ነው ማለታቸው ነው? ወይስ ገና ሊፈቱ ቅድመ ዝግጅት እያደረጉ? ወይስ ምንም ማለታቸው አይደለም? የሚገርመው ደግሞ ጋዜጠኛውም ማብራርያ አለመጠየቁ ነው፡፡ ለሌላ ተመሳሳይ ጥያቄ ደግሞ “እኔ እንደተኬደበት ነው የማውቀው” ብለዋል - ከንቲባው (የማወሳሰብ ጥበብ ይሏል ይሄ ነው) ሌላው በጣም ያስገረመኝ ---- ከንቲባው ብዙዎቹን የከተማዋን ችግሮች ከጋዜጠኛው የሰሙ መምሰላቸው ነው፡፡ (የአራዳ ልጅ ናቸው ብያችሁ የለ!) እናም ጋዜጠኛው ስለአንድ ጉዳይ ሲጠይቃቸው “እንዲህ ያለ ነገር ተፈፅሞ ከሆነ በጣም አሳፋሪና ህገወጥ ተግባር ነው! አጣርተን --” የሚል ምላሽ ይሰጣሉ፡፡ እንዲህ የሚሉት ደግሞ አንዴ እኮ አይደለም - በተደጋጋሚ ነው፡፡ “ግን እኮ 10 ዓመቱ ነው--- አልዘገየም?” ሲል ጋዜጠኛው መልሶ ይጠይቃቸዋል፡፡ ከንቲባውም ልስልስ ባለ አንደበት “አዎ አዎ እሱ ልክ ነህ ---- በጣም ዘግይቷል!” ይሉላችኋል፡፡ (ነገሩን ለማረጋጋት እኮ ነው!) ካፌና ሱፐርማርኬት እንገነባለን በሚል መሬት የወሰዱ ባለሀብቶች 10 ዓመት ሙሉ ምንም ሳይሰሩ አጥረው መቀመጣቸውን ሲያነሳባቸው ምን ቢሉ ጥሩ ነው? “እንዲህ የሚያደርጉትንማ እያየን እርምጃ የመውሰድ ግዴታ አለብን!” (እኮ መቼ?) ይቅርታ አድርጉልኝና ---አንዳንድ የመንግስት ሹማምንት ተደብቀው ወደ አዳዲሶቹ አገራት (ደቡብ ሱዳንና ሶማሊያ) ጐራ እያሉ የትርፍ ሰዓት ሥራ ሰርተው የሚመለሱ እየመሰለኝ ነው (ዶላር ሊያምራቸው ይችላላ!) እኔ የምላችሁ ---- በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል እስከ ቅርብ ዓመታት ድረስ የክልሉ መንግስት ባለስልጣናት ስድስት ወር ቤተመንግስት ሲያስተዳድሩ ቆይተው፣ ስድስት ወር ደግሞ መሳሪያ ታጥቀው ከኦብነግ ጋር የኢትዮጵያን መንግስት ሲወጉ እንደከረሙ ሰምታችኋል?(ጦቢያ እኮ ያልተሸከመችው ጉድ የለም!) ምን ይሄ ብቻ---ብሔራዊ መዝሙራቸውም ታላቋን ሶማሊያ የሚያወድስና ጦቢያን የሚራገም እንደነበር የክልሉ ፕሬዚዳንት መናገራቸው ተዘግቧል፡፡ (በአንድ ልብ ሁለት ዜግነት ማለት እኮ ነው!) በነገራችሁ ላይ በቅርቡ የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልልንና ሌሎች ምስራቃዊ የአገሪቱን ክፍሎች ጐብኝተው የመጡ አንዳንድ አርቲስቶች “የክልሉ ፕሬዚዳንት ሃይለኛ ኮሜዲያን ናቸው!” በማለት ሲያደንቋቸው ሰምቻለሁ፡፡ እሱስ ባልከፋ ነበር። ስለአመራራቸው ምንም አለማለታቸው ግን ትዝብት ላይ ይጥላል፡፡

አርቲስቶች ዋዛ ፈዛዛ ብቻ ነው እንዴ የሚያውቁት ያስብላል እኮ፡፡ ለዚህ ሳይሆን አይቀርም በጉብኝቱ ወቅት “አርቲስቶች” እና “አትሊስቶች” የሚል ሁለት ጐራ የተፈጠረው፡፡ (የግል ግምቴ ነው!) ሌላው በትልቁ የታሙበት ጉዳይ ምን መሰላችሁ? ከባለስልጣን ጋር የመሞዳሞድ ምኞትና ጉጉት ታይቶባቸዋል ይላሉ - የሙያ ባልደረቦቻቸው፡፡ በየክልሉ መሬት ይሰጠን የሚል ጥያቄ ማቅረባቸውም ለሃሜት ዳርጓቸዋል (እንኳን ሊሰጣቸው ቃል ባይገባላቸውም) እኔ ግን የመሬቱ ጥያቄ ለሃሜት የሚያበቃ አይደለም ባይ ነኝ (አንዳንዴ እንደ ዳያስፖራ ቢያደርጋቸውስ?) አሁን ደግሞ “የብርሃናችንን ጌታ” በደንብ እንቦጭቀው - የኢትዮጵያ መብራት ሃይል ኮርፖሬሽንን ማለቴ ነው፡፡ ባለፈው ረቡዕ ቀላል ተጫወተብን መሰላችሁ? ተማረን ከአገር እንድንሰደድ ከሆነ እርሙን ቢያወጣ ይሻለዋል --- ህዳሴ ግድብ ሳያልቅ ከጦቢያ ንቅንቅ አንልም፡፡ እንዴ --- በአንድ ተሲያት በኋላ ብቻ እኮ ስምንት ጊዜ መብራት ጠፍቷል (በታሪኩ አዲስ ሪከርድ መሆን አለበት) በነገራችሁ ላይ በተመሳሳይ ሰዓት ኢትዮ ቴሌኮምም ኔትዎርክ አልነበረውም - እናም እርስ በርስ እየተደዋወልን ንዴታችንን መወጣት እንኳ አልቻልንም፡፡

አሁን አሁን ስለ ታላቁ ህዳሴ ግድብ ሳስብ ስጋት የሚፈጥርብኝ ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? የግብፅ ጉዳይ ከመሰላችሁ ተሳስታችኋል! ግብፅማ አመነች እኮ - እጅ ሰጠች፡፡ አሁን ችግሩ ያለው እዚሁ ነው - አፍንጫችን ሥር! ይኸውላችሁ --- የታላቁ ህዳሴ ግድብ ተጠናቆ አገልግሎት ሲጀምር ማነው የሚያስተዳድረው የሚለው በጣም ነው ያሳሰበኝ፡፡ መንግስት ኮርፖሬሽኑ ያስተዳድረዋል ብሎ ካሰበ እድሜ ልኩን “ይቅርታ” ሲጠይቅ መኖር አምሮታል ማለት ነው፡፡ ሃይል እንሸጥላቸዋለን የምንላቸው አገሮች እኮ እንደኛ ዝም የሚሉ አይደሉም (እኛ እኮ ችሎ ነዋሪ ስለሆንን ነው!) እኔ የምላችሁ --- የዝነኛውን ፓርላማችንን አብዮት እያስተዋላችሁልኝ ነው? (ታላቅ የታሪክ ክስተት እንዳያመልጣችሁ!) ይሄው እንግዲህ ፓርላማችን የድሮ ታሪኩን አውልቆ ጥሎ ሚኒስትሮቹን ማፋጠጥ፣ መጠየቅ፣ መፈተሽ ወዘተ-- ገፍቶበታል። (የሰይጣን ጆሮ አይስማብን!) እኔማ ባለፉት 20 ዓመታት ያሁኑን ግማሽ ያህል እንኳ ቢንቀሳቀስ ኖሮ ስንት ሥራ በተሰራ እያልኩ መቆጨቱ ሊገለኝ ነው። (የፈሰሰ ውሃ አይታፈስም!) የመንግስትና የግል ሌቦች መጫወቻም አንሆንም ነበር እኮ፡፡

በነገራችሁ ላይ ሰሞኑን ጠ/ሚኒስትሩ ከባለሃብቶች ጋር ባደረጉት ውይይት “ለራሳችንም ሆነ ለግል ሌቦች አንራራም” ማለታቸውን ማጤን ተገቢ ነው፡፡ (የድሮዋ ጦቢያ መስላኝ ነው ብሎ መፀፀት አያዋጣም) ወደ ፓርላማው ስንመለስ -- ባለፈው ሳምንት ለምክር ቤት አባላት ሪፖርት ያቀረቡት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ሃላፊው “በሰብዓዊ መብት ትንሽ ወደ ኋላ የተጓተትንበት ሁኔታ ያለ ይመስለኛል። የውጭዎቹ ሜዳውን የራሳቸው አድርገው የተጫወቱበት ሁኔታ ነው ያለው” ሲሉ ተናግረዋል። በዚህ ከቀጠልን እኮ እነ“ሂዩማን ራይትስ ዎች” ሰብዓዊ መብት ተጥሷል ምናምን እያሉ አይወቅሱንም - እኛው ራሳችን ቀድመን መጣሱን እናምንላቸዋለና። እኔ የምላችሁ ግን --- ኢህአዴግ አሁንም ምስጢረኛነቱን አልተወም ማለት ነው፡፡ ቢተውማ ኖሮ--- በፓርላማችንና በኢቴቪ አሰራር እየታየ ያለው መነቃቃት ከምን የመጣ እንደሆነ በግልፅ ይነግረን ነበር፡፡ ራሳቸው የፓርላማ አባላቱም እኮ “ፓርላማው ጥርስ እያወጣ ነው?” ለሚለው ጥያቄ መች በአግባቡ መልስ ሰጡን - “እኛ ድሮም ሥራችንን በአግባቡ ነው የምንወጣው” ከማለት በቀር! በዚህ አጋጣሚ ኢቴቪም የህዝብ ንብረትነቱን ለማረጋገጥ የሚያደርገውን መፍጨርጨር ልናደንቅለት ይገባል።

(ቡዳ እንዳይበላው መፀለያችንን ሳንረሳ!) በነገራችሁ ላይ ፓርላማው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ስለፈጠረው ታላቅ አብዮት ለመናገር ብንሞክርም --- ሁሉም በመሸምጠጡ እኛ ያየነውን አይቻለሁ የሚል ሁነኛ ሰው ከየት እናገኝ ይሆን እያልኩ ሳስብ ነበር፡፡ ባሳለፍነው ሳምንት ግን ከ “ሰንደቅ” ጋዜጣ ጋር ቃለ ምልልስ ያደረጉት አንጋፋው የህወሃት መስራች አቦይ ስብሃት ምስጋና ይግባቸውና ሃቃችንን አረጋገጡልን፡፡ አቦይ “የፌደራል ዋና ኦዲት ሪፖርት ለእርስዎ የሚሰጥዎት ትርጉም ምንድነው?” በሚል ተጠይቀው ሲመልሱ “በዚህ አገር በዚህ ስርዓት በአሁኑ ጊዜ ትልቁና የማያጠራጥር ተስፋ ሰጪ ሁኔታ የፌዴራል ዋና ኦዲተር ጠንከር ያለ እንቅስቃሴ መጀመሩና ከሁሉም በላይ ደግሞ የፌደራል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህዝብ ተወካይነቱን ማረጋገጥ መጀመሩ ነው፡፡ ይህ ከፍተኛ የስልጣን አካል ሥራ መጀመሩ ለኢትዮጵያ ህዝብ ትልቅ የምስራች ነው” ብለዋል፡፡ እኔ ደግሞ በዚህ የምስራች ለፓርላማው አባላት በሙሉ የወጣቱን ድምፃዊ የይሁኔ በላይን “እልል በይ አገሬ---” የሚል ዜማ ጋብዤአቸዋለሁ። በዚህ አጋጣሚ አንድ ሃሳብ አለኝ፡፡ ፓርላማው ነፃነቱንና የህዝብ ተወካይነቱን የተቀዳጀበት ወር ለምን በየዓመቱ አይከበርም? (ሌላ ግንቦት 20 ማለት እኮ ነው!)

Saturday, 29 June 2013 09:49

የትግራይ ጉዞ ማስታወሻ

ተናጋሪዋ ምድር

ሰኔ 8 ቀን 2005 ዓ.ም ጠዋት፡፡

ዕለቱ በከፍተኛ ጉጉት ሲጠበቅ ነበርና ከቀጠሮው ቦታ የተገኘሁት ልክ ከንጋቱ አስራ አንድ ሰዓት ላይ ነው፡፡ ምክንያቱም ቡድኑ በጥዋት ተነስቶ ረጅም መንገድ መጓዝ ይጠበቅበታል፡፡ ከአዲስ አበባ ለመነሳት ገስግሶ መሰባሰብ ያስፈልጋል ስለተባለ የቀጠሮው ጊዜ ከንጋቱ አስራ አንድ ሰዓት ነበር፡፡ በርካታ ተጓዦች በተባለው ሰዓት ቢገኙም አንዳንድ ተጓዦች ግን በመንገድ መዘጋት (በዚያ ሰዓት መንገድ ተዘጋ ማለት አሳማኝ ባይሆንም) እና በተመሳሳይ ሰበቦች ጊዜ ባለማክበራቸው የመነሻ ሰዓት አልተጠበቀም፡፡ በዚህም ቀድመው የተገኙ አባላት መነጫነጭና መወቃቀስ ጀምረው የነበሩ ሲሆን በተለይ አስተባባሪዎቹ ተበሳጭተው እንደነበር አስተውያለሁ። የብስጭታቸው ሰበቡ “ለምን ሰዓት አይከበርም? ለምን የአበሻ ቀጠሮ እያልን ራሳችንን ስንዘልፍ እንኖራለን?” የሚል ነው፡፡ 11፡30 ላይ ከአዲስ አበባ ለመነሳት ተይዞ የነበረው ቀጠሮ በ1፡30 ተራዝሞ ልክ ከጥዋቱ አንድ ሰዓት ላይ ጉዞው ተጀመረ፡፡ ጉዞው የጥበብ ጉዞ ነው፡፡

“የዓባይ ዘመን ሕያው የጥበብ ጉዞ ሶስት ወደ ቅዱስ ያሬድና ፈላስፋው ዘርዓያዕቆብ ሀገር” በሚል መሪ ቃል የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር ያዘጋጀው ታሪካዊ ጉዞ። ሙሉ ወጭውን የሸፈነው ደግሞ የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ነው፡፡ የኪነጥበብ ሰዎች በሆነ ምክንያት ቢጋጩ እንኳ ቁጣቸው የሕፃን አይነት ቁጣ በመሆኑ ወዲያው ይረሱታል፡፡ የጥበብ ተጓዦችም በአርፋጆች ላይ እንዲያ ሲነጫነጩ እንዳልነበረ ሁሉ አዲስ አበባን እንደለቀቅን ዘፈኑና ትረባው ተጀመረና በሁሉም ተጓዦች ፊት ላይ የደስታ ስሜት ይነበብ ጀመር። ተጓዦች 43 ሲሆኑ በርካታውን ቁጥር የያዙት ደራስያን ናቸው፡፡ የግልና የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች፣ ሃያስያን፣ የስነ ጽሑፍ መምህራንና ተመራማሪዎች እንዲሁም ሰዓሊያንና ከማህበሩ ጋር በቅርበት የሚሰሩ ማተሚያ ቤቶች ተወካዮችም የጉዞው አካላት ናቸው፡፡ የዕድሜ፣ የሥራ፣ የዕውቀትም ሆነ የጾታ ልዩነት መኖሩ ባይካድም በተሳፈርንበት የዓለም 1ኛ ደረጃ አውቶብስ ውስጥ የነበሩት ተጓዦች ሁሉ ዕኩዮች ይመስሉ ነበር።

የፈለገ ይዘፍናል፤ ያሻው ያቅራራል፤ ሌላውም ወይ ገጠመኙን ያወራል፤ ወይም ግጥም ያነብና ተጓዡን ያዝናናል፡፡ እንዲህ እንዲህ እያለ ጉዞው ቀጠለና በ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በተመሠረተችው ጥንታዊቷ የደብረ ብርሃን ከተማ ቁርስና ምሳ አንድ ላይ ተበሉ፡፡ አንዳንድ ተረበኞች “ቁምሳ” ብለው በአህጽሮተ ቃል እንደሚናገሩት መሆኑ ነው፡፡ ከቁርስ በኋላ ሁካታውና ጨዋታው በእጅጉ ደርቶ ሰሜናዊው ጉዞአችን ቀጠለ፡፡ የጣርማ በርን ዋሻዎች፣ አናቷ ላይ ጉም የማይለያትና የጠመጠመ ቄስ የምትመስለዋን ደብረ ሲናን፣ ኤፍራታን፣ ሸዋሮቢትን፣ ማጄቴን፣ ካራቆሬን፣ ከሚሴን፣ ሐርቡንና ኮምቦልቻን አቆራርጠን በ19ኛው ክፍለዘመን የንጉሥ ሚካኤል ከተማ ከነበረችው ደሴ ላይ ሻይ ቡና አልን፡፡ በነገራችን ላይ አዲስ አበባ ብቻ ሳትሆን የዞን ከተሞችም በእጅጉ መነቃቃታቸውን ማስተዋል ችያለሁ፡፡ ከተመሰረተች ከ573 ዓመት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረችው ደብረ ብርሃን እንደ ኦሪታዊው አቤሜሌክ አንቀላፍታ እንዳልኖረች ሁሉ፣ ዛሬ የዘመናዊ ህንፃዎችና ጐዳናዎች ባለቤት ሆና ማየት “ይበል” የሚያሰኝ ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡

በ15ኛው ክፍለ ዘመን በጉንዳጉንዶ መነኮሳትና በአፄ ዘርዓያዕቆብ መካከል በነበረው የሃይማኖት እሰጥአገባ ምክንያት የሀገራችን ሥነጽሑፍ ጣራ ደርሶ የነበረው በዚች ታሪካዊት ከተማ ነበር፡፡ ልጅ በዕደ ማርያም ዙፋን ከወረሰ በኋላ ግን ደብረ ብርሃን ክብሯም ስሟም በአያሌው ተጐሳቁለው ነበር። የሀገሪቱ ዋና ከተማነቷ ሲቀር በስልጣኔ መራመድ አቅቷት መፍገምገሟ ግድ ሆነ፡፡ አሁን ግን የሚታይ ለውጥ እያስመዘገበች ነው ብሎ በድፍረት መናገር ይቻላል፡፡ ከሚሴም በአማራ ክልል የኦሮሞ ዞን ዋና ከተማ ከሆነች በኋላ እየተነቃቃች መሆኑን ተገንዝቤያለሁ። በነገራችን ላይ የጠቀስኋቸውንም ሆነ ወደፊት የማነሳሳቸውን ከተሞችና አካባቢዎች ቀደም ብዬ ስለማውቃቸው ነው ለውጥ አለ ብዬ መመስከር የፈለግሁት፡፡ ኮምቦልቻ መልክዓምድራዊ አቀማመጧ ስለሚያግዛት ዘመናዊ ከተማ የመሆን ዕድሏ ሰፊ ነው። “የአሰብ መንገድ መስተጓጐል በንግዱ ማህበረሰብ ላይ የተወሰነ ተጽእኖ ይፈጥራል” የሚል ስጋት የነበረ ቢሆንም ከተማዋ እንዲያውም ከታስበው በላይ ፈጥና የተጓዘች ትመስላለች፡፡ ዘመናዊ የአውሮፕላን ማረፊያ እየተገነባላት ሲሆን ከጐጃም ጋር በየብስ የሚያገናኛት መንገድ ግንባታም እየተጠናቀቀ በመሆኑ ለዕድገቷ ተጨማሪ ጉልበት ይሆናታል፡፡ የጦሳ ተራራ መፈናፈኛ ያሳጣት ደሴም አሮጌ ልብሷን አውልቃ እየጣለች በተሃድሶ ላይ ትመስላለች፡፡ የቦታ ጥበት እያለም ደሴ በለውጥ ላይ ናት፡፡ አሮጌና ደሳሳ ቤቶች በዘመናዊ ህንጻዎች እየተተኩ ናቸው፡፡ ግን አሁንም የጦሳ ተራራ አናቷ ላይ ሆኖ ቁልቁል ይኮረኩማታል፡፡ ጦሳን በደን መሸፈን ካልተቻለ እና ለተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ትኩረት ካልተሰጠው የደሴ ተስፋ ረጅም ጉዞ ላይዘልቅ ይችላል፡፡

ከዚህ ቀደም በተግባር የታየ ነገር ስላለ ከእሱ መማር ብልህነት ይመስለኛል፡፡ ከደሴ ከተማ በ30 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኘዋና በሃገራችን ታሪክ ቀዳሚው ከፍተኛ የትምህርት ተቋም የነበረባት ታሪካዊቷ የሃይቅ ከተማም እየተስፋፋች መሆኑን ታዝቤያለሁ፡፡ ጉዞው ቀጥሏል፤ ቀኑ እየተገባደደ ስለሆነ መፍጠን አለብን፡፡ ጭፈራውም፣ መዝናናቱም ቀጥሏል፡፡ የአምባሰልን ሰንሰለታማ ተራሮች እየቃኘን ስንጓዝ አስተባባሪው ድንገት ተነሳና ዝም እንድንል ጋበዘን “በግራ በኩል ከምታይዋት ደልዳላ ቦታ ላይ ነው ያ መዘዘኛ ውል የተፈረመው፡፡ አፄ ምኒሊክ ከጣሊያኑ ወኪል ጋር የውጫሌን ውል የፈረሙት ከዚያ ቦታ ላይ ነው፤ ስሙም ይስማ ንጉሥ ይባላል” ሲለን ቦታዋን የማያውቋት ደራስያንና ጋዜጠኞች የሰሙትና የሚያዩትን ማስታወሻቸው ላይ በፍጥነት ያሰፍሩ ጀመር፡፡ አሁን ጨዋታው ሁሉ ቆመና ውጫሌ የውይይት ርዕስ ሆነች፡፡ የአምባሰል ተራራ እንደ ጆፌ አሞራ በላይዋ ያንዣበበባት ውጫሌ የዕድሜዋን ያህል አላደገችም፡፡ አምባሰልም ራቁቱን ነው፡፡

የኪነጥበብ ሰዎች “አምባሰል ለገደል ምን ያሽሟጥጡታል ፈረስ ባያስጋልብ ማር ይቆርጡበታል” እንዳላሉት ሁሉ ዛሬ ገጽታው አስፈሪ ነው፡፡ እንኳን ለንብ የሚሆን አበባ ያለው ዛፍ ለምልክት ቢፈለግም የሚገኝበት አይመስልም፡፡ ስለዚህ የዞኑ ህዝብና መንግስት ልዩ ትኩረት ቢሰጡትና በደን ቢሸፈን የአምባሰል ውበት፣ የአምባሰል ወዘና የማይመለስበት ምክንያት አይኖርም፡፡ ሆኖም አምባሳል የተጓዦችን ስሜት ሰቅዞ መያዙ አልቀረም፡፡ ውርጌሳ ያው ናት፤ መርሳ መጠነኛም ቢሆን ለውጥ አላት፡፡ ሲሪንቃ የእርሻ ምርምር ጣቢያ ለአካባቢው ውበት ቢሆንም የታሰበውን ያህል እየሰራ መሆኑን መናገር አልቻልሁም፡፡ በጉዞ ላይ ሆኜ ነዋ ያየሁት፡፡ በነገራችን ላይ ከዚህ በኋላም ስለሚጠሩት ከተሞችና አካባቢዎች የምሰጠው አስተያየት ሳልፍ ባስተዋልሁት መረጃ ላይ ተመስርቼ መሆኑ ልብ ይባልልኝ፡፡ መኪናችን ክንፍ ባይኖረውም ይከንፋል፡፡

በጊዜ ወልድያ ለመግባት ከፍተኛ ፍላጐት የነበረን ቢሆንም ሲሪንቃ ላይ ጐማ ተነፈሰና እኛም ተናፈስን፡፡ አመሻሽ ላይ 521 ኪሎ ሜትሮችን አጠናቀን ወልድያ ገባንና አዳር እዚያው ሆነ፡፡ ዙሪያዋን የከበቧት ተራሮች ባይገድቧት ወልድያም በዕድገት ለመመንጠቅ እየተንደረደረች መሆኗን ተገንዝቤያለሁ፡፡ የሁለተኛው ቀን ጉዞአችን ቀጥሏል፡፡ ጉዞው ደግሞ ወደ ሰሜን ነው፤ ወደ ቅዱስ ያሬድና ፈላስፋው ዘርዓያዕቆብ ሀገር፡፡ በጥዋቱ ከወልድያ ተነስተን ጐብየን “እንዴት ነሽ?” ብለናት ቆቦ ላይ እረፍት አደረገን፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ከመቀሌ የሚመጡ እንግዶች ስለነበሩ ትንሽ ጊዜ መጠየቁ የግድ ስለሆነ ነው፡፡ ራያዎች፣ አማራዎች፣ ትግሬዎችና አፋሮች በፍቅር የሚኖሩባት ቆቦ፤ በጥዋቱም ሞቅ ደመቅ እንዳለች ነው ያገኘናት፡፡

አዳዲስ ህንፃዎች ለቆቦም እንግዳዎች አይደሉም፤ እዚያም እዚህም ተስፋ ሰጭ ጅምሮች ይታያሉ፡፡ የቆቦ ቆይታችን በሻይ ቡና ከተጠናቀቀ በኋላ ዞብልን በርቀት እያየን ጉዞ ወደ ትግራይ ክልል ሆነ፡፡ ትረባው፣ ዘፈኑ፣ ግጥሙ፣ ተረቱ….አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡ ልክ የአማራን ክልል እንደጨረስን አንድ ፒክአፕ መኪና በፍጥነት ቀደመንና ቪዲዮ ካሜራ የያዙ ወጣቶች አውቶብሳችንን ይቀርጽ ጀመር። ለጊዜው ማንነታቸውን ባንለያቸውም የኋላ ኋላ የክልሉ መገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች መሆናቸውን ተረድተናል፡፡ ከአላማጣ ከተማ ወጣ ብሎ በርካታ መኪኖችን ስናይ መንገድ የተዘጋ መስሎን ጉዟችንን ሊያጓትትብን ነው የሚል ስሜት ተፈጠረብን፡፡ እየተጠጋን ስንሄድ ደግሞ መንገዱ በመኪና ብቻ ሳይሆን በርካታ ባጃጆች ጭምር ተዘጋግቷል፡፡

መዘጋጋት ብቻ ሳይሆን የከበሮ፣ የዕንቢልታ፣ የዕልልታና የጥሩንባ ድምጽ በአያሌው እያስተጋባ ጠበቀን፡፡ ማለፍ ስለማንችል መኪናችንን አስጠግተን መቆም ግድ ሆነ፡፡ እኛ ስንቆም ዕልልታውና ጭፈራው ይበልጥ ድብልቅልቁ ወጣ፡፡ መኪኖችና ባጃጆችም በጥሩንባዎቻቸው አካባቢውን አደመቁት፡፡ ግራ ተጋብተን ሳለ የትግራይ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ፍስሃየ አለማየሁና የክልሉ ባህል ቱሪዝም ኤጀንሲ ኃላፊ አቶ ከበደ አማረ ከመኪና እንድንወርድ ነገሩን፡፡ ከመኪና መውረድ ስንጀምር ዕልልታውና ዘፈኑ እጅግ ደመቀ፡፡ ለካ ያ ሁሉ የመኪናና የባጃጅ ሰልፍ፣ ያ ሁሉ ዕልልታና ደስታ፣ ያ ሁሉ ደማቅ ሰልፍ ለጥበብ ተጓዦች የተዘጋጀ አቀባበል ኖሯል፡፡ ከመኪናችን እንደወረድን በባህላዊ አልባሳት የተዋበ ህዝብ ከቦን ጭፈራውን ያቀልጠው ጀመር፡፡ አቀባበሉ ለአንድ የሀገር መሪ እንጂ ለኪነጥበብ ሰዎች የተደረገ አይመስልም፤ አላማጣ ቄጠማ ጐዝጉዛ፣ ፈንዲሻ እየበተነች በልጆቿ ውብ ዜማና ጭፈራ ከሰርግ በደመቀ ሁኔታ ተቀበለችን፡፡ እውነት ለመናገር የህዝቡን ሁኔታ ሳስተውል እንባዬን መቆጣጠር አቅቶኛል፡፡ አቀባበሉ ከአንገት በላይ አይደለም፤ ከንፁህ ልብ ስር በመነጨ ፍቅር የታጀበ መሆኑን እንደ እኛ በቦታው የተገኘ ብቻ ሊያየውና ሊመሰክር ይችላል፡፡

አላማጣ አቀባበል ያደረገችልን በሆታና በእልልታ ብቻ አይደለም፤ በከንቲባዋ በአቶ ገብረ ትንሣኤ ፍሥሐ አማካይነት የእንኳን ደህና መጣችሁ አቀባበል ከሞቀ ቁርስና የቡና ስርዓት ጋር ቀርቦልን ተዝናንተናል፡፡ ከዚህ ሌላ ያለ ዕድሜው በድንገት በተለየን በኢያሱ በርሄ ስም የመሰናዶ ትምህርት ቤት መሰየሙን ተረዳንና አላማጣ ለኪነጥበብ ሰዎች ተገቢውን ክብር እንደምትሰጥ አረጋገጥን፡፡ አብረው የተጓዙ የቅኔ ሊቃውንትም የአላማጣ ህዝብ ስላሳየን ጥልቅ ፍቅር ቅኔ ዘረፉ፤ ተጓዡንም አዝናኑ፡፡ መቀሌ ገብተን ማደር ይጠበቅብናልና መፍጠን አለብን፡፡ ስለሆነም ራያዎች የሚዙበትን አላማጣን መሰናበት ግድ ሆነ፡፡ ጐልጐል ራያን (የራያ ሜዳ) አልፈን ጥቂት ኪሎ ሜትሮች ወደሰሜን እንደተጓዝን፣ የግራ ካሱ ተራራ እናት ዶሮ ጫጩቶቿን ከጭልፊት ለመታደግ በአክናፍዋ እንደምትሸፍናቸው እኛንም ከሆነ አደጋ ይጠብቀን ይመስል በጉያው ወሸቀን።

ግራ ካሱ “ገራህት ካሱ/የካሱ እርሻ” የሚል መነሻ እንዳለው አቶ ከበደ አማረ ነግረውናል፡፡ ግን ግራ ካሱ ቀጥ ያለ ግን ደግሞ ሰንሰለታማ ተራራ ነው፡፡ ከጥቂት ዓመታት በፊት ግራ ካሱ ጥርሱን ያገጠጠ፣ አለቱ የፈጠጠ ተራራ ነበር፡፡ ከዚህ ሌላ በቀድሞው መንግሥትና በህወሓት መሃል ዘግናኝ ጦርነቶች እንደተካሄዱበት ተረድተናል፡፡ ዛሬ ግን ግራ ካሱ በእርስ በርስ ጦርነት የሚያፏጭ አረር አይሰማበትም፤ ዛሬ የሁለት ወንድማማቾች በድን እንደአልባሌ ዕቃ የትም ወድቆ አሞራ አይጫወትበትም፤ ይልቁንም ህይወትን በሚታደግ ውብ ነገር ተሸፍኗል - በተፈጥሮ ደን፡፡ ከግራ ካሱ ተራራ ልጆች ሊማሩት የሚገባ ዐቢይ ቁምነገር አለ፤ እሱም ተፈጥሮ ልክ እንደሰው ልጆች ነፃነትዋን የምትሻ መሆንዋን ነው፡፡ የክልሉ ባለስልጣናትና ነዋሪዎች ያደረጉት ነገር የለም። ያደረጉት ቢኖር አካባቢውን ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ነፃ ማድረግ ብቻ ነው፡፡ በዚህ የተነሳ ያ ጣረሞት ይመስል የነበረ ተራራ በተፈጥሮ ደን ተሸፍኖ የዱር እንስሳት መፈንጫና ቀልብን የሚስብ መሆን ችሏል፡፡ ይህ ለብዙ የአገራችን አካባቢዎች ብቻ ሳይሆን ለሌሎች የምስራቅ አፍሪካ አገሮችም አብነት የሚሆን ይመስሉኛል፡፡ ጉዞውም ጽሑፉም ይቀጥላል፡፡

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

ይኸው ሰኔም ልትወጣ ነው…ሐምሌም ሊገባ ነው…ዓመቱም ሊያልቅ ነው! ይለቅማ! ስሙኝማ…ዘንድሮ ራስን ሆኖ ከመገኘት ይልቅ የታየዘው ምን መሰላችሁ…‘ኢምፕሬስ’ ማድረግ፡፡ (‘ኢምፕሬስ’ የምትለው የገባችው ጨዋታ ለማሳመር እንደሆነ ልብ ይባልልን…) እናላችሁ…የነገሮችን ስሞች እንደቀለበት መንገድ ማሽከርከር፣ በተለይ ሁሉ ነገር ውስጥ የ‘ፈረንጅ አፍ’ ሸጎጥ ማድረግ የተለመደ ‘ኢምፕሬስ’ ማድረጊያ ዘዴ ሆነውላችኋል፡፡ ‘የምናምን ድርጅት የሰው ሀይልና የፕሮጀክት ትግበራ የሥራ ሂደት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር…’ አይነት “ትንፋሽ እየወሰዳችሁ…” የምትጠሩት ስም አይሰለቻችሁም! ኮሚክ ነገር እኮ ነው…ከሰውየው የሥራ ሀላፊነት ዝርዝር ይልቅ እኮ የማዕረግ ስሙ ሊረዝም ምንም አይቀረው! (ስሙኝማ…ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… አንዳንድ የሥራ ሀላፊዎች ጠረዼዛ ላይ ፊት ለፊታቸው የሚቀመጠውንና ስማቸውንና ሀላፊነታቸውን የሚገልጽ ጽሁፍ አይታችሁልኛል! የምር እኮ… ግዙፍነቱ …አለ አይደል…“ተሳስተው የመሥሪያ ቤቱን መጠሪያ ከዋናው በር ነቅለው አምጥተውት ነው እንዴ!” ያሰኛል፡፡

አሀ… ከመተለቁ የተነሳ አንዳንዴ የሀላፊውን ከረባት እርፍናና ቅሽምና ማየት አልቻልንማ! ቂ…ቂ…ቂ… እኔ የምለው… ሥራ ይቀላጠፍ፣ ዙሪያ ጥምጥም ነገር ይቅር በሚባልበት ዘመን አንድ መስመር ጨርሶ ሁለተኛ መስመር የሚያጋምስ የማዕረግ ስም አጻጻፍ ከየትኛው የበለጸገ አገር የወሰድነው ተሞክሮ ነው! (ስሙኝማ…ይሄን ሁሉ ነገር ከበለጠጉ አገሮች ተሞክሮ እየወሰድን በ‘ፎቶኮፒ’ ለራሳችን እንደምናውለው…“ምን አለ እኛ የኮረጅነውን ነገር የፈጠሩበት አእምሯቸውን በወሰድን…” አያሰኛችሁም! ‘ቦተሊከኞች’ ሆይ… “ከበለጸጉ አገሮች የወሰድነው…” ማለት ‘ደረት እንደማይስነፋ’ ልብ ይባልሉንማ! እናማ…“ከበለጸጉ አገሮች የወሰድነው…” ማለት ምን ይመስለኛል መሰላችሁ… ‘ኢምፕሬስ’ ለማድረግ! ስሙኝማ…አሁን አንዳንድ ፊልሞቻችንን ነገሬ ብላችሁ እንደሆነ በአማርኛ ቋንቋ ተሠርተው ፖስተሮቻቸው በእንግሊዝኛ የተሞሉ ናቸው፡፡ አማርኛው ኖሮ እንግሊዝኛው በተጓዳኝነት ቢኖር ይገባችኋል…ግን ፊልሙ ውስጥ..አለ አይደል…ከቦሌ እስከ ጉለሌ ሁላችን የምንሞክራት ‘ሁዋሳ’ፕ’ የምትለዋን የ‘ፈረንጅ አፍ’ በሌለችበት ፊልም የእንግሊዘኛ ድርድር… ግርም አይላችሁም! ኮሚኩ ነገር ምን መሰላችሁ… ጠጋ ብላችሁ ፖስተር ላይ የተጻፈውን ስታነቡ…አለ አይደል…“ይቺን እንኳን ያለስህተት መጻፍ አይቻልም!” ያሰኛችኋል፡፡

እናማ…ይሄ ሁሉ ለምን መሰላችሁ… ‘ኢምፕሬስ’ ለማድረግ! ስሙኝማ እግረ መንገዴን…ፊልሞች የአማርኛ ቃለ ምልልሶችን በእንግሊዝኛም በግርጌ ጽሁፍ ማቅረባቸው (‘ሰብታይትል’ የሚባለው) አሪፍ ነው፡፡ ግንማ… የ‘ፈረንጅ አፏ’ ኘላይ ባትሆን እንኳን መሰረታዊ ስዋሰው ምናመን ነገር ይታሰብበት! አንዳንዴማ በየፖስተሩና በየ‘ሰብታይትሉ’ ላይ ያሉትን ስህተቶች ስታዩ…አለ አይደል…“ከሼክስፒር ትያትሮች ወዲህ እንግሊዝኛ ላይ ስር ነቀል ለውጥ የተካሄደው በፊልሞቻችን ፖስተሮችና ‘ሰብታይትሎች’ ነው…” አይነት ነገር ያሰኛችኋል፡፡ እናማ ይሄ ሁሉ ለምን መሰላችሁ…‘ኢምፕሬስ’ ለማድረግ! ስሙኝማ…ይሄ የ‘ፈረንጅ አፉን’ በሆነ ባልሆነው ቦታ በመሸጎጥ ‘ኢምፕሬስ’ ማድረግ የእኛ የተራዎቹ ነገር ብቻ ሳይሆን ‘ወደላይም’ ከፍ፣ (ኧረ ‘በጣም ከፍ’!) ይላል፡፡ ይኸውና… ኧረ እባካችሁ ‘ትራንስፎርሜሽን’ ለሚለው አቻ አማርኛ ቃል አይጠፋም እያልን ባለንበት ሰዓት…‘ሌጌሲ’ ተጨምራ አረፈችው! (ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…በየቦታው ‘ሌጌሲ’ የምትለዋን በየመፈክሩ ላይ የሚከቱ ሰዎች አንዳንዶቹ “ለመሆኑ ሌጌሲ የምትለዋ ቃል ትርጉሟ ምንድነው?” ቢባሉ የሚሰጧቸው መልሶች ለቲቪ ዝንቅ ፕሮግራም የሚሆኑ አይመስላችሁም! ከሚሰጡት መልስ አንዱ ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…“ሂድና የበላይ አካልን ጠይቅ!) እናማ ይሄ ሁሉ ለምን መሰላችሁ…‘ኢምፕሬስ’ ለማድረግ! እናላችሁ…ይሄ ‘ኢምፕሬስ’ የማድረግ አባዜ ማለቂያ ያለው አይመስልም፡፡ በየመንደሩ እየተቋቋሙ ያሉት የማህበረሰብ ቢጫና ጥቁር ኮንቴይነር ቤቶች ላይ የተጻፈውን ልብ ብላልችሁልኛል? ‘…ፖሊስ ጣቢያ…’ ከማለት ይልቅ የተጻፈው ‘…ፖሊስ እስቴሽን…’ የሚል ነው፡፡ (ሀሳብ አለን…‘…ፖሊስ እስቴሽን…’ የሚለው ቃል የማይቀርልን ከሆነ ‘እስቴሽን’ የምትለዋ ቃለ ውስጥ ‘እ’ የምትለው ፊደል ወይ ትወገድልን… ወይም “ማን የጻፈውን ማን እናቱ የወለደችው ያስወግዳል!” ከተባለ ‘ትዋጥልንማ’! ቂ…ቂ…ቂ… እናማ ይሄ ሁሉ ለምን መሰላችሁ…‘ኢምፕሬስ’ ለማድረግ! እኔ የምለው…የስም መርዘም ወይም የ‘ፈረንጅ አፍ’ መክተት እኮ ለነገርዬው ተጨማሪ ‘ክብደት’ አይሰጠውም፡፡ አባቶቻችን ‘መልከ ጥፉ በስም ይደገፉ…’ የሚሏት ነገር አይነት ነው፡፡ አሁን ደግሞ ይሄ የፌስቡክ ዘመን አይደል…ፌስቡክ የሌለው ሰው ልክ እኮ በ‘ድንጋይ ዘመን’ እንዳለ ሰው ሊቆጠር ምንም አይቀረው፡፡

እናላችሁ… ኤፍ ኤሞች ላይ በርካታ ፕሮግራሞች “ፌስቡክ ገጻችን ላይ ላይክ አድርጉን…” ሲሉ እየሰማን ነው፡፡ ‘ላይክ’ እንድናደርጋችሁ የሁላችሁንም ፎቶ ለጥፉልንማ! አሀ…‘ላይክ’ የሚደረገው ገጹ ይሁን ወይም ከገጹ ጀርባ ያሉት ሰዎች ግልጽ ይደረግልና! ስሙኝማ…እግረ መንገዴን ይቺን ስሙኝማ… ልጅቷና ሰውየው የተዋወቁት ፌስቡክ ላይ ነው፡፡ እና በአካል ሊገናኙ ይቀጣጠራሉ፡፡ ታዲያላችሁ…እሷዬዋ አሪፍ እንትናዬ ሆና ቀጠሮው ቦታ ስትጠብቅ የሆነ ሰው ይመጣል፡፡ እናማ… “እንዴት ነሽ?” ምናምን ሲላት እሷ ሆዬ በልቧ “ምን አይነቱ ደረቅ ሰው ነው?” ምናምን እያለች ሳለች…ሰውየው ማን መሰላችሁ…የፌስቡከ ጓደኛዋ! ለካስ በፌስቡክ ‘ፕሮፋይል ፎቶው’ ሸበላና የብራድ ፒትን የቶም ክሩዝ ‘ሪሚክስ’ የሚመስለው ሰውዬ በአካል ሲታይ የእኔ ቢጤ ዘፍዝፈው ያሳደሩት በቤተሰቡ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ የአልጋ ልብስ ይመስላል! እናላችሁ…እሷዬዋ “ፕሮፋይል ፒክቸርህ ላይ ሌላ ነህ?” ትለዋለች፡፡ እሱዬው ምን ቢል ጥሩ ነው… “በፎቶሾፕ አሳምሬው ነዋ!” እናማ…እንትናዬዎች… የፌስቡክ ‘ፕሮፋይል ፒክቸር’ ሁሉ እውነት መስሏችሁ እንዳትታለሉማ፡፡ የእኔ ቢጤዎቹ “ሰው ቢጠይቀን ምን ብለን እንመልሳለን?…” በሚል ፌስቡክ ገጽ የከፈትን ፎቶ የማንለጥፈው እኮ ፎቶ ስለሌለን ሳይሆን…“ማን እጅ ይሰጣል!” በሚል ነው፡፡

ልጄ አንዳንዴ ብልጥነት እኮ ወንዝ ያሻገራል፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…የብልጥነት ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ስሙኝማ… በጋብሮቮ መንገድ ላይ ሲያለቅስ የነበረ አንድ ልጅ የገጠመው አንድ ለጋስ ሰው ልጁን “ለምንድነው የምታለቅሰው?” ይለዋል፡፡ ልጁም “አንድ ብር ጠፋብኝ” ሲል ይመልሳል፡፡ ሰውየውም “በቃ፣ አታልቅስ” ብሎ አንድ ብር ይሰጠዋል፡፡ ልጁ ግን ብሩን ከተቀበለ በኋላ ማልቀሱን ይቀጥላል፡፡ ሰውየውም “አሁን ደግሞ ምን ሆንኩ ብለህ ነው የምታለቅሰው? ብር ሰጠሁህ አይደል እንዴ!” ይለዋል፡፡ ልጁ ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው...“አንዷ ብር ባትጠፋ ኖሮ ሁለት ብር ይሆንልኝ ነበር፡፡” ልጁ ጋብሮቮያዊ ነዋ! እናላችሁ…በየቦታው የምታዩት ‘ኢምፕሬስ’ የማድረግ ሙከራ ወደ ኮሜዲነት እየተለወጠ ነው፡፡ እናማ…የፈረንጅ አፍ መክተት፣ ስምን “መንገዱ ረዘመ፣ ረዘመ…” አይነት ማስረዘም…“ሂድና ሞኝ ቱሪስት ብላ!” የሚሉ ‘ነቄ’ ሰዎች እንዳሉ ማወቁ አሪፍ ነው፡፡ እስካሁን ድረስ ‘ኢምፕሬስ’ የምትለዋን የ‘ፈረንጅ አፍ’ ደጋግሜ በመጠቀም የምርም ‘ኢምፕሬስ ካላደርግኋችሁ’… አለ አይደል…‘ነቄ’ ብላችኋል ማለት ነው፡፡ እንደ ፌስቡክ ፕሮፋይል ፒክቸር መሆኑን ነቅታችሁብኛል ማለት ነው፡፡ ‘“ማሞ ሌላ መታወቂያ ሌላ…” እንደተባለው፡፡ ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል
Page 2 of 17