“እስኪ ተጠየቁ” የተሰኘው የዮሐንስ አድማሱ የግጥም መድበል ነገ በ8 ሰዓት በብሄራዊ ቤተ መፃሕፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ውይይት ይደረግበታል፡፡ለውይይቱ መነሻ ሃሳብ የሚያቀርቡት አርክቴክትና ደራሲ ሚካኤል ሽፈራው እንደሆኑ ታውቋል፡፡ውይይቱን ያዘጋጁት እናት የማስታወቂያ ድርጅት፣ ጀርመን የባህል ማዕከልና ብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ-መፃሕፍት ኤጀንሲ በጋራ ሲሆን የሥነፅሁፍ ቤተሰቦች በውይይቱ ላይ እንዲገኙ ጥሪ ቀርቦላቸዋል፡፡

 

     የገጣሚ ኃይሌ ተስፋዬ ቸኮል የግጥም ስብስቦች የተካተቱበት “የራዕይ እግሮች” የተሰኘ የግጥም መድበል ነገ ከጧቱ 3፡00 ጀምሮ በፍፁም ሲኒማ ይመረቃል፡፡ የግጥሙ ይዘት ማህበራዊ፣ መንፈሳዊና ፖለቲካዊ ትዝብት ላይ የሚያተኩር ሲሆን የግዕዝን ቋንቋ በመቀላቀል በጠንካራ አገላለፅ የታጀበ ነው ተብሏል፡፡

ገጣሚው ግጥም ወደመፃፍ የተሳበበትን ምክንያት በመድበሉ መግቢያ ላይ ሲያስረዳ፤ “ገና በ11 ዓመቴ አካባቢ ቤተክርስቲያን ስማር የእነሙሴን፣ ዳዊትን … ረዣዥም ግጥሞች ከመፅሀፍ ቅዱስ ቃል በቃል እገለብጥ ነበር፡፡ ይህ የህይወት ልምምድም እድሜዬ እየጨመረ በመጣ ጊዜ ትልቅ ዕርዳታ አድርጎልኛል” ብሏል ገጣሚው፡፡ በ110 ገፆች የተቀነበበው መድበሉ፤ 73 ግጥሞችን ያካተተ ሲሆን ለአገር ውስጥ በብር 35.50፣ ለውጭ ደግሞ በ15 ዶላር እንደሚሸጥ ታውቋል፡፡ 

 

 

 

 

በዘመናዊ ቴክኖሎጂ፣ በምቹ ወንበሮችና ከውጭ አገራት በገቡ የተለያዩ መሳሪያዎች የተደራጀው “ሶሎዳ ቪአይፒ ሲኒማ” በከተማዋ እምብርት አራት ኪሎ፣ ዴንቨር ታዎር ላይ ከትላንት በስቲያ ተመርቆ ተከፈተ፡፡በቪአይፒ ደረጃ የታነፀው ሲኒማ ቤቱ፤ በአንድ ጊዜ ውስን የተመልካች ቁጥር እንደሚያስተናግድ ተገልጿል፡፡

ሲኒማ ቤቱ የተከፈተበትን ምክንያት ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ ያብራራው ድርጅቱ፤ በሃገራችን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሲኒማ ኢንዱስትሪ ላይ እየታየ ያለውን መነቃቃት ከግምት ውስጥ በማስገባትና የማህበረሰባችንን አፍቅሮተ ጥበብ በመገንዘብ መሆኑን አስታውቋል፡፡

 

 

 

 

 

 

 

 

 

ላለማሰብ እያሰብኩኝ

በጨለማ ተቀመጥኩ

የልቤን ሆደ ባሻነት ገሰፅኩኝ

ተስፋ መቁረጥን ተስፋ አደረኩኝ፡፡

    ይኼንን “የወሌፈንድ” ፍልስፍና ቁልጭ አድርጐ የሚያሳይ ግጥም የፃፈው ታላቁ ባለቅኔ ደበበ ሰይፉ ነው፡፡ “ተስፋ መቁረጥን ተስፋ ስለማድረግ” ለመረዳት ቀጥተኛ አስተሳሰብን መጠቀም አያገለግልም፡፡

ግጥሙ የዘመኔን መንፈስ ገላጭ ነው፡፡

ጆርጅ ኦርዌል በዓብይ ስራው “1984” ላይ ይኼንን የአስተሳሰብ መንገድ “Double think” ሲል ይገልፀዋል፡፡ ሁለት ጊዜ ስለ አንድ ነገር ማሰብ ማለት ነው፡፡ ግን ሁለት ጊዜ የታሰበው ነገር ሁለት ሊታረቁ የማይችሉ ተቃርኖዎችን ወደ በአንድ አጣምሮ ለማሰብ ቢያስችልም፤ ግን የእውነትን ማንነት ከውሸት ጋር ቀይጦ ሁለቱንም ወጥ ነገሮች የሚያጠፋም ነው፡፡

ደርቦ ማሰብ (double think) እንደዚህ ይገልፀዋል ኦርዌል፡- “To know and not to know, to be conscious of complete truthfulness while telling carefully constructed lies, to hold simultaneous two opinions which canceled out, knowing them to be contradictory and believing in both of them, to forget whatever it was necessary to forget…” እያለ ይቀጥላል፡፡

ይኼንን ፅንፍ ተቃርኖን የማቀላቀያ የአስተሳሰብ መንገድ (Double think) ለማስተናገድ የሰው ተፈጥሮ በጣም አመቺ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ውሸትን ከእውነት ጋር አቻችሎ የማሰብ ብቃት አለን፡፡ አጣምሮ የሚያስበው ግን ሁለቱንም ነጣጥሎ ትክክለኛ ባህሪያቸውን ለመረዳት ሲል ማጣመር እና የማጣመር አባዜ ስለተጠናወተው  ብቻ መሆን ትልቅ ልዩነት ይፈጥራል፡፡

በአጭሩ፤ “ተስፋ ማድረግ” መልካም መሆኑን አውቆ፤ ተስፋ መቁረጥን ለመቀነስ “ሁለቴ የሚያስብ” ከሆነ ይህ እውነተኛው አማራጭ መሆኑን መቀበል እናም ተግበር አንዱ (በእኔ እምነት ትክክለኛው አማራጭ) ነው፡፡ ላለማሰብ ማሰብን መርጦ… ተስፋ መቁረጥን ተስፋ ማድረግ ደግሞ ሌላው ነው፡፡

ከጀርመን እንዲያሊዝም በተለይም ከሄግል ያገኘነው አንዱ መጥፎ ነገር (እንደኔ እምነት)…የማይጣመሩ ነገሮችን የማጣመር ፍላጐትን ነው፡፡ ሄግል - Thesis (አዎንታዊ) ከUntithesis (አሉታዊ) ጋር ሲደመር አዎንታዊ እና አሉታዊውን ወደፊት የሚያሳድግ አዲስ የድብልቅ አማራጭ ይገኛል ባይ ነው፡፡ ይሄንኑ የሄግል ፅንሰ ሐሳብ (አይዲያሊዝሙን ወደጐን ትተው) የተጠቀሙበት የግራ ዘመም ርዕዮት ያላቸው ሃይሎች ናቸው፡፡

የማርክስ ዲያሌክቲካዊ ማቴሪያሊዝም… ከሄግል ዲያሌክቲካዊ አይዲያሊዝም የተወሰደ ነው፡፡

አዎንታዊ (ለምሳሌ እውነት፣ ተስፋ፣ ማወቅ፣ ማሰብ፣ ብርሃን) ከአሉታዊው ጋር ሲቀየጥ “ወሌፈንድ” ይፈጠራል፡፡ “ላለማሰብ ማሰብ” ፣ “ተስፋ መቁረጥን ተስፋ ማድረግ”… “Double think” የዚህ ውጤት ነው፡፡

ለምሳሌ በሀገራችን “አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች” የሚባሉ የጐሳ አየነቶች አሉ፡፡ በኦርዌላዊ “ጥምዝ ሃሳብ” የተካኑ ስለመሆናቸው አንዳችም ጥርጣሬ የለኝም፡፡ የሚሰጡት አስተያየት ውሸትም፣ እውነትም እንደሆነ በአንድ ቅፅበት አውቀው ነው በቴሌቪዥን ለመናገር የሚቀርቡት፡፡ በእውነተኛ ቁርጠኝነት ውሸትን ለመግለጽ ወይንም በእውነት እውነትን ለመቅበር ሃሳባቸውን አለማምደውታል፡፡

የሚናገሩት ነገር ውሸት እንደሆነም… እውነት ስለመሆኑም አውቀው ነው የሚናገሩት፡፡ እውነት እና ውሸትን ቀላቅሎ ማሰብ የተማረ አዕምሮ የተማረውን ቀላቅሎ መናገር መቻሉ አያጠያይቅም፡፡

“Double think” በውስጥ የሚዳብር የአስተሳሰብ መንገድ “Double Speak” ደግሞ በውጭ የሚቀርብ መገለጫው ነው፡፡ ሳይንሳዊ መንገድን በመጠቀም እውነትን መግለጽ፣ ሳይንሳዊ እውነታን መፍጠር ቀደም ብሎ ሲያስችል ቆይቷል፡፡ ሳይንሳዊ መንገድን በመጠቀም መዋሸት ግን ሳይንሳዊ እውነታን በሳይንሳዊ ውሸት አደናግሮ ለማሳመን ፍቱን መድሃኒት ነው፡፡

እውነትና ውሸትን በእኩል (በእኩይ) መንገድ መቀላቀል መቻል የሰውን አእምሮ ለማደንዘዝ በጣም አቋራጩ መንገድ ነው፡፡

ምሳሌ ልስጥ፤ “የሰው ልጅ በምንም አይነት በሌላ የሰው ልጅ መገደል የለበትም” የሚል ጽንሰ ሃሳብ በስነምግባር ፍልስፍናም ሆነ በሃይማኖት አስተሳሰብ ድጋፍ ሊኖረው ይችላል፡፡ እውነት ተብሎም ተቀባይነት አግኝቷል እንበል፡፡

“የሰው ልጅን ለመግደል የሚያሴሩ ስላሉ ለብዙሀኑ የሰው ልጅ ሲባል ጥቂቶቹ መገደል ይኖርባቸዋል” ከተባለ… አሁንም ብዙ ድጋፍ እና ጭብጨባ ይገኛል፡፡

አዎንታዊው ሃሳብ ከአሉታዊው ጋር በመቀላቀሉ የሰው ልጅን የሚጠብቅ እና የሚገድል አዲስ ሃይል ይፈጠራል፡፡ ይኸም ሀይል ባለስልጣን ሆኖ በመጠበቅ ስም የመግደል ሃላፊነትን በህጋዊ ቢሮ መልክ ይረከባል፡፡

ዣን ጃክ ሩሶ ከዘመናዊ የፖለቲካ ፈላስፎች መንገድ ጠራጊ አድርገው ምዕራባዊያን ይቆጥሩታል፡፡  በብዙሀን አንደበት ውስጥ በቀላሉ Popular የሆነ አባባል አለው፡፡ ምናልባት አባባሉ በመጽሐፉ (The social contract) የመጀመሪያው ገጽ ላይ በመገኘቱ ምክንያት ሊሆን ይችላል በቀላሉ የታወሰለት…

ለማንኛውም “Man is born free but every where in chains” ይላል፡፡ የሰው ተገቢ የማንነት ስፍራ ነፃነት ቢሆንም ያለ አግባብ በጭቆና ተጠፍሮ ዘወትር ይገኛል ማለቱ ነው፡፡ ሁለቱን ተቃራኒዎች አዎንታዊውን (ነፃነት) ከአሉታዊው (ባርነት) ጋር ቀላቅሎ ቢገልፃቸውም… ሁለቱን የቀላቀላቸው አትክክል የሆነውን ካልሆነው አንፃር አንጥሮ ለማውጣት እንጂ የማይደባለቁትን ሰይጣን እና መልአክ አጋብቶ ለማስማማት አይደለም፡፡

ተቃራኒዎችን አነፃፅሮ ማሰብ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ነው፡፡ ነጭ እና ጥቁርን ደምሮ እና ቀንሶ …በስተመጨረሻ ለያይቶ ፍቻቸውን ተረድቶ መግለጽ ጤናማ ተፈጥሯችን ነው፡፡ ጥበባችን፣ ፈጠራዎችን፣ ሳይንሳችን፣ የአስተውሎታችን መነሻ እና መድረሻ በዚህ ሂደት ውስጥ ያለ ነው፡፡

የሄግል ዲያሌክቲክስ እና የኦርዌል “Double think” ግን ከዚህ የተፈጥሮ ህጋችን ያፈነገጠ ነው፡፡ ጥቁር እና ነጭን ደባልቆ… ግራጫ ከጥቁር እና ከነጭ የበለጠ መሆኑን የሚናገር ነው፡፡ ማለትም “ተስፋ መቁረጥን ተስፋ ማድረግ” በተናጠል ማንነት ከነበራቸው “ተስፋ ማድረግ” እና “ተስፋ መቁረጥ” የበለጠ ነው እንደማለት፡፡

(ወይንም በሰሞኑ ሁኔታ ደግሞ በእርግጥ ከተገኘ ለውጥ ይበልጥ በእርግጥ የተገኘ የሚመስል የለውጥ ማስረጃ እድገት ነው እንደማለት ነው፡፡)

“Double think” በጥበብ አለም (በፈጠራ አለም) ስኬት ነው፡፡ በጣም እውነት የሚመስል ውሸትን መስራት የደራሲው ስኬት ነው፡፡ ገሃዱ አለምን ቁልጭ አድርጐ የሚያሳይ ነገር ግን በገሀዱ ተከስቶ የማያውቅ ፈጠራ “ውሸት ነው” ተብሎ ተአማኒነት አያጣም፡፡ ምክንያቱም፤ ጥበብ እውነትን የሚያጐላ ውሸት ነውና፡፡ እንዲያውም “መስታወቴ” ብሎ ተደራሲ የራሱን ውሸት በራሱ ጓዳ ከእውነቱ ጋር እያመሳከረ ህፀፁን እንዲያርም ያግዘዋል፡፡ (ወይንስ በጥበብ አማካኝነት የገሃድ አለምን ህመምን ማረም ወይንም መፈወስ የቻለ እስካሁን አንድም ከያኒ የለም? አከራካሪ ነጥብ ነው)

ያም ሆነ ይህ ጥበበኛው የራሱን ሃሳብ እና የገፀባህሪውን ሃሳብ ደብሎ መናገር እና ማሰብ ይችላል፡፡ ችግር የሚመጣው ከጥበብ ዘርፍ ውጭ ያሉት የገሃዱ አለም ግንኙነቶችም በዚሁ የጥበብ ውሃ ልክ በመሰለ ወለፈንድነት መመራት (መተግበር) ሲጀምሩ ነው፡፡

የትያትር መድረክ ላይ ትያትረኛው አንድን ገፀ ባህርይ ወክሎ ያስባል፤ ይናገራል፡፡ ከመድረክ ሲወርድ ግን እንደ እውነተኛ ማንነቱ ማሰብ እና መናገር መቻል አለበት፡፡ ጥበበኛው በፈጠራ ወቅት “Double think” ሲያደርግ ከሰውኛ የገሃድ ስነምግባሩ ጋር መጋጨትም የለበትም፡፡

ለመድረክ ላይ የሚጫወተውን ገፀ ባህርየ በገሀዱ አለም ላይም የሚደግም ሰው “የጥበብ ዲያሌክቲክስ” ፈጥሬአለሁ ካለ ችግር ነው፡፡ ልክ ድሮ የመድረክ ተዋናይ የነበረ ሰው በአጋጣሚ የአዕምሮ ጤናው ተቃውሶ በጐዳና ላይ ከወጣ እና ለብዙ አመታት ከተጐሳቆለ በኋላም “ፕርፎርመንስ አርት እየሰራ ነው” ብለው እንደተናገሩት ማለቴ ነው፡፡ እውነት እና ውሸት… ምክንያታዊነት እና እብደት የሚጣመሩበት ጊዜ እና የሚለያዩበት ወቅት ካልታወቀ ወለፈንድነት ለሙሉ ጊዜ በእውነታው አለም ላይ የማያቋርጥ ተውኔት ለማካሄድ ለባብሶ መድረክ ላይ ወጥቷል ማለት ነው፡፡ መድረኩ ደግሞ ትያትር ቤት ሳይሆን እለት ተለት ህይወት ትሆናለች፡፡

“Double think” የሚለውን የኦርዌል ሃሳብ ከሄግላዊ ማታፊዚክስ ጋር አንድ መሰረት አለው እያልኩ ነው፡፡ መሰረቱ ደግሞ ለአንባገነን ስርዓቶች እና ከብዙዎች ላብ አትርፈው ለተደላደሉት ጥቅም ይሰጣል ባይ ነኝ፡፡

በተጨማሪ የጥንቱ ካፒታሊዝም እና የጥንቱ ኮሚውኒዝም በዚሁ መንገድ ነው ተቀላቅለው የቻይናን ቴክኖሎጂ የፈጠረችውን ምዕራብ እና የምዕራብን ገበየ የፈጠረችውን ቻይና ወለፈንድ አድርገው ማስማሙት፡፡

“አለም ትያትር ናት ትያትር ደግሞ አለም”

ከትያትሩ የሚያተርፈው ተዋናዩ አይደለም ትያትር ቤቱ እንጂ፡፡ ሁሉም ትያትር ቤቶች የመንግስት ናቸው፡፡ በሁሉም ትያትር ቤት ተመርቀው የሚከፈቱ ፊልሞችን ህዝብ ራሱ ተውኖ ራሱ ይመለከታል፡፡ ራሱ ተውኖ ራሱ የተመለከተውን ራሱ ይከፍላል፡፡ የሚከፍለው በገንዘቡ ብቻ ሳይሆን በህይወቱም በቀጣይ የተስፋ ጭላንጭሉም ጭምር ነው፡፡ተዋናይ ነኝ ወይንስ ተመልካች?ደራሲ ነኝ ወይንስ ተደራሲ፣ ድራማው ተጠናቋል ወይንስ መጀመሩ ነው (ለሃያ አራት አመት መጀመሪያው ምዕራፍ ፈቅ የማይል ድርሰትም የወለፈንድ የድራማ ዘውግ ነው) ጭብጡ ጨለምተኛ ነበር ወይንስ ብርሃናማ? “አንዳንድ የአ.አ ከተማ ነዋሪዎች እነማን ናቸው? እኔ እና ማን ናቸው? “Man is born free but every where in chains በሚለው የሩሶ ሃሳብ እና በመሀመድ ስልማን “Man is borne in China but is found every where” በሚለው ሽሙጥ መሃል ምንም ለውጥ ይጠፋል፡፡

ግራ እና ቀኝ ሃሳቦች፣ እውነት እና ውሸት ተደባልቀው አንድ ይሆናሉ፡፡ እግዜር (Malevolent)፣ ሰይጣን (benevolent) በዴያሌክቲካዊ መንገድ ግራጫ ይሆናሉ፡፡ ግራጫ “Ambivalent” ነው፡፡ ላለማሰብ እንደማሰብ ነው ግራጫ ወይንም ስለሞት ሲባል መናር፡፡

የግራ ዘመም እና የቀኝ ዘመም ድብልቅ ወደየትም አይዘምም፡፡ ቢዘምም የዝመቱን አቅጣጫ የሚያነፃፅርበት… የማይለዋወጥ ቋሚ መለኪያ አይኖረውም፡፡ እርስ በራስ የሚጠፋፋ ሁለት ተቃራኒ ሃሳቦች አጋጭቶ እያስማማ… ሲስማማ እየጋጨ የድምር ዜሮ… የእውር ድንብር ጉዞ ማድረግ ብቻ ነው ውጤቱ፡፡

ገጣሚ ቢኒያም ዋሲሁን ግራና ቀኝ እጄ ተጣልተው ሲጋጩ “ጭብጨባ” ተብሎ ተተረጐመ እንዳለው… ግጭት ድጋፍ መስሎ ተቀባይነት ያገኛል፡፡

ይኼንን የወሌፈንድ አዝማሚያ “የሰው ልጅ ሞት” ብዬ ነው የምቆጥረው፡፡ ግን ወሌፈንድን ለመረዳትም የ “Double think”  አስተሳሰብን መከተል ያስፈልጋል፡፡

እየሞተ ያለው የሰው ልጆች አለም “እያደገ ነው” ሲባል ምን ማለት እንደሆነ በትክክል ለማወቅ… እውነት ከውሸት ጋር እንዴት ተቀይጦ በግራጫ ቀለም እንደፀደቀ መረዳት ግድ ይላል፡፡  

 

 

 

 

Published in ጥበብ

     በዚህ እትም የምናስነብባችሁ አንድ ገጠመኝን ነው፡፡ በሕክምናው ዙሪያ ያጋጠማቸውን እውነታ ያወጉን አቶ አምቢበል ታረቀኝ ሲሆኑ የገጠመኙ ባለታሪክ ወ/ት ናርዶስ እምቢበልም የጠቀሰችውን ለንባብ ብለናል፡፡

‹‹...እንዲያው ይህ ሰው የት ነበር? ያሰኘኝ አንድ ነገር ነው፡፡ ልጄ በአንድ ወቅት ድንገት መነሳት መቀመጥ አቃተኝ ትለኛለች፡፡ እኔና ባለቤቴም በመጀመሪያ እቤት ውስጥ በጋለ ድንጋይ በፈላ ውሃ በመሳሰሉት ብናሞቃት ምንም ለውጥ አልተገኘም፡፡ በሁዋላም በወጌሻ አስሞከርናት፡፡ ወጌሻው አሁን ትድናለች እያሉ ለሰባት ቀን ወገብዋን እያገላበጡ እያሹልን ተሸክመን ወደ ቤት እናመጣለን፡፡ ነገር ግን እርስዋ ምንም ሊሻላት አልቻለም፡፡ ከዚያም ወደ ሐኪም ቤት መሔድን ተመካከርንና ወደሶስት የሚሆኑ የግል እና የመንግስት ጤና ተቋማት ወሰድናት፡፡ ሁሉም የተለያየ ምክንያት እየሰጡ መድሀኒት ያዙናል፡፡ ነገር ግን  መፍትሔ ሊሆን አልቻለም፡፡

አንዳንዶች ከጨጉዋራ ጋር ያያይዙታል፡፡ ሌሎች ደግሞ ጣፊያሽ ተቃጥሎአል በረሀ ነው እንዴ የምትኖሪው? ይላሉ፡፡ አንዱ ሐኪም ደግሞ ማህጸንሽን ተመርመሪ ኢንፌክሽን ሊሆን ይችላል አለ፡፡ ጭርሱንም ጉበትሽን ታዪ ጉበት ሳይሆን አይቀርም ያለን ሐኪም ተስፋ አስቆረጠን፡፡ ምክንያቱም ጉበትዋን እስክትታይ ድረስ በሚል የሰጣትን መድሀኒት ስትወስድ ሌሊቱን ሙሉ ተቃጠልኩ ስትል አሳደራት፡፡

እኔና ባለቤቴ ተመካከርን፡፡

በቃ ፡፡ ከዚህ በሁዋላ ወደ ሐኪም ቤት አንሞክርም፡፡ ጸበል ነው የምንወስዳት ብለን በሶውንም ዳቦቆሎውንም ማዘጋጀቱን ጀመርን፡፡ ለጸበሉም እጣ ስናወጣ አንዲት ጎረቤታችን የታማሚዋን ውሎ አዳር ለመጠየቅ አመሻሹ ላይ መጣች፡፡..

እንደምን አመሻችሁ?

እግዚአብሔር ይመስገን፡፡ ግቢ ግቢ...

እየተቀባበልን ጋበዝናት፡፡

ናርዶስ አንዴት ነች?

አረ ምንም አልተሸላት፡፡

ትንሽም አልተሸላት?

ጭርሱንም ብሶባታል፡፡

እንዴት?

በቃ፡፡ ሐኪሞቹ ምንም አላወቁላት፡፡ እኛም ሰለቸን፡፡

ምንድነው የተጠቀለለ ወረቀት ጠረጴዛውን የሞላው?

በቃ፡፡ ከዚህ በሁዋላ ሐኪም ምን ያደርግላታል፡፡ ያልወሰድንበት ቦታ የለም፡፡ ወጌሻው አልቀረ ሐኪሙ አልቀረ፡፡ ሁሉም ምንም መፍትሔ አልሰጡዋትም፡፡ ጭርሱንም እየባሰባት መጣ፡፡ ይኼው እንግዲህ ወደ ስድስት ወር ሆናት፡፡ እርስዋ ጭርሱንም ምግብ መብላት እያቆመች መጣች፡፡

ምን ታድርግ? መቀመጡ እያስቸገራት ነዋ፡-

አዎን ፡፡ እኛም ገብቶናል፡፡ አይዞሽ ...ምንም ችግር የለም ብንላትም ...እርስዋ ግን ልትቀበለው አልቻለችም፡፡

እና ታድያ ምን ልታደርጉ አሰባችሁ?

በቃ...ይኼው እንደምታይው እጣ ጥለን ወደ ጸበል ልንወስዳት እየተዘጋጀን ነው፡፡ እንዲያውም አንቺ እንኩዋን መጣሽ ...እጣውን ታወጪልናለሽ፡፡

ጥሩ፡፡ ነገር ግን እኔ እጣውን ከማውጣቴ በፊት አንድ እድል ይሰጠኝና ልሞክር፡፡

ምን ትሞክሪያለሽ?

ሐኪም ጋ ልውሰዳት፡፡

አይ...አይ...አይ...እኛ ስንት ጋ ወስደን የታከተንን ደግሞ አንቺ እንደገና ወደሐኪም ትወስጃለሽ? አይቻልም፡፡

እንዴ..እኔ እኮ ልጅቷ የልጆቼ ጉዋደኛ ...ባልወልዳትም ልጄ ነች፡፡ ስለዚህ ፍቀዱልኝ፡፡

የለም የለም አታሰናክይን፡፡ ይልቁንም እጣውን አውጭልን፡፡

ግድየለህም የናርዶስ አባት... ለአንድ ሁለት ቀን እኮ ነው፡፡ እናንተ ስንቃችሁን ልብሳችሁን እስክታዘጋጁ ድረስ እኔ በመሀከል ወደ ሐኪም ልውሰዳት እና ከውጤቱ      በሁዋላ ትወስዱዋታላችሁ፡፡

በዚህ መሀከል ባለቤቴ አስታራቂ ሆና ፈቀደችላት፡፡ ያች ሴትዮ በማግስቱ ከባለቤቷ ጋር ሆና በመኪናቸው ወደ ሐኪም ቤት ሲወስዱዋት ..አንድ ሰው ብቻ ታማሚዋን እንዲደግፋት ሰጠናቸው እንጂ እኛ አልተከተልናቸውም፡፡ ልጅትዋ ታክማ ስትመለስ ያየችውን እንዲህ ነበር ያወጋችን፡፡

...ወደ ሐኪሙ ጋ ስገባ ልክ አስቀድሞ ለብዙ ጊዜ እንደሚያውቀኝ ነበር ሰላምታው፡፡ እንደምንድነሽ ናርዶስ...? ሲለኝ ገና ልቤ ወከክ ነበር ያለው፡፡ እኔም ስቅቅ ብዬ ሳልቀመጥ እንደቆምኩ ...በማይሰማ ድምጽ...ደህና...ደህና ነኝ... ነበር ያልኩት፡፡ በእርግጥም እናንተ እንዳላችሁትም እኔም ወደ ሐኪም ጋ መሔድን ሰልችቼው ነበር፡፡ ያመጡኝን ሴት ማለትም የጉዋደኞቼን እናት አክብሬ እንጂ እኔም አምቢ ብል ደስ ይለኝ ነበር፡፡

ከዚያም...አይዞሽ አትፍሪ... ምንሽን ነው የሚሰማሽ? የሐኪሙ ጥያቄ ነበር፡፡ እኔም እንጃ...ከማህጸኔ ነው መሰል... መቀመጥ መተኛት አልቻልኩም... በማለት መለስኩለት፡፡ ማህጸንሽን ከአሁን ቀደም ታመሽ ታውቂያለሽ? ወይንስ በምን ጠረጠርሽ?

አ...አ...አይ... ሐኪሞቹ እንዲያውም ሌላም ሌም በሽታ ይኖርብሽ ይሆናል አሉኝ እንጂ በትክክል ይህ ነው በሽታሽ አላሉኝም፡፡ እስቲ ነይ እዚህ መተኛ ላይ... ብሎ ወደ መመርመሪያ አልጋው ሄድ አለ፡፡ ...እኔም በግድ ተነስቼ ከአልጋው ለመውጣት ሞከርኩ፡፡ ግን አልቻልኩም፡፡ ሐኪሙ ግን በጣም ደግና እሩህሩህ ስለነበር.. አይዞሽ ...እኔ እረዳሻለሁ ብሎ... ከመመርመሪያው አልጋ ላይ አሳረፈኝ፡፡ ከዚያም ምርመራውን ሲያደርግ... በማህጸኔም በመጸዳጃዬም በኩል ሲፈትሽ ሳላስበው ከልክ በላይ ጮህኩኝ፡፡ በቃ ተነሽ አለኝ እና ከአሁን በፊት ወድቀሽ ታውቂያለሽ አለኝ፡፡ አዎን ግን በጣም ቆይቶአል... አልኩት፡፡ ቢቆይም የህመምሽ ምክንያት እርሱ ነው፡፡ በዚያ ምክንያት መቀመጫሽ ወይንም ጭራሽ አካባቢ የተጎዳ ነገር አለ፡፡ ለማንኛውም ቀላል ነው፡፡ ይህንን መድሀኒት አሁኑኑ መውሰድ ጀምሪ ብሎኝ ተለያየን፡፡...

 የልጅቷ ታሪክ ይኼው ነው፡፡ ለስድስት ወር ያህል አልጋ ያልለቀቀች ልጅ ...መድሀኒቱን ስትወስድ በሶስት ቀን ተነስታ ወዲያ ወዲህ ማለት ጀመረች፡፡ እኔም በጣም አዝኜ... ሴትየዋን እግዚያብሄር ይስጥልኝ ከማለት ይልቅ እንደዚህ ያሉት ሐኪሞች ምናለ ብዙ ቢሆኑ? ለመሆኑ ይህ ሰው የት ነበር? ስል አፈጠጥኩባት፡፡.. የሚል ነው የአቶ እምቢበል ታረቀኝ ገጠመኝ፡፡

በሚቀጥለው እትም የህክምና ባለሙያዎች እውቀታቸውን ...ክህሎታቸውን እንዴት በየጊዜው ማደስ እንዳለባቸው ስለወጣው አሰራር የምናስነብባችሁ ይኖራል፡፡

 

Published in ላንተና ላንቺ

 

 

 

በሳምንቱ አጋማሽ ላይ የዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር 7 አመራሮች በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በኤፍቢአይና በስዊዘርላንድ ፖሊስ ቅንጅት በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡ ዓለምአቀፉ የእግር ኳስ ማህበር በሙስና ቀውሱ የገቢና የክብር ኪሳራ እንደደረሰበት በመገለፅ ላይ ነው፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ፕሬዝዳንት ፕላቲኒ፣ የፈረንሳይና የእንግሊዝ እንዲሁም የአሜሪካ ባለስልጣናት ሴፕብላተር ከስልጣን እንዲወርዱ ጠይቀዋል፡፡

የራሽያው ፕሬዝዳንት ፑቲን አሜሪካ ዜጎቿ ባልሆኑ ሰዎች ላይ የወሰደችው እርምጃ ጣልቃ ገብነት ብለው ሲያወግዙት፤ ማራዶና በበኩሉ ባንድ ወቅት የፊፋን አመራሮች ስግብግብ ሙሰኞች ናቸው ብሎ ሲናገር እንደእብድ መቆጠሩን አስታውሷል፡፡ ፊፋ በካዝናው እስከ 1.5 ቢሊዮን ዶላር አካብቶ በዓለም እግር ኳስ ግን ከ150 ዶላር በታች ገቢ ያላቸው ተጨዋቾች አሉ የሚለው ማራዶና አሁን ያለው የፊፋ አመራር ያለአንዳች ቅድመሁኔታ ከስልጣን መውረድ እንዳለበት ተናግሯል፡፡

 ብላተርና የፕሬዝዳንት ምርጫው

ሰሞኑን ከተፈጠረው ቀውስ ጋር በተያያዘ 65ኛው የፊፋ ኮንግረስ ጉባዔ እና የፕሬዚዳንት ምርጫው መካሄዱ አጠያያቂ መስሎ ነበር፡፡

የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር አባል አገራቱ በዚሁ የምርጫ ሂደት ላይ እንዳይሳተፉ የጠየቀ ሲሆን በሌሎች ክፍለዓለማት የሚገኙ አገራትም ሁኔታውን በጥርጣሬ እየተመለከቱት ሰንብተዋል፡፡

በፊፋ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ላይ የ79 ዓመቱ ሴፕ ብላተር ለ5ኛ ጊዜ እንደሚመረጡ የተጠራጠረ አልነበረም፡፡  ብላተር አስተዳደራቸው በሙስና ወንጀሎች በተናጠበት ወቅት ለ5ኛ ጊዜ በፕሬዝዳንትነት ለመመረጥና ፤በእስራኤልና በፍልስጤም ፌደሬሽኖች መካከል እርቅ ለመፍጠር ትኩረት አድርገው ሰንብተዋል፡፡ ከመረጣችሁኝ በሚቀጥለው የስራ ዘመኔ ለፊፋ የተንሰራፋውና ችግር ለመቅረፍ እችላለሁ በሚልም ቃል ገብተዋል፡፡

የፊፋ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ላይ ስድስት ኮንፌደሬሽኖች 209 አገራትን በመወከል ይሳተፋሉ፡፡ 54 አገራት ከአፍሪካ ዞን፤ 53 አገራት ከአውሮፓ ዞን፤ 46 አገራት  ከኤሽያ ዞን፤40 አገራት ከሰሜንና መካከለኛው አሜሪካ ፤ 10 አገራት ከደቡብ አሜሪካ ዞን፤ 11 አገራት ከኦሽኒያ ዞን ናቸው፡፡ ሴፕ ብላተር በይፋ ድጋፋቸውን ከገለፁላቸው ከአፍሪካ እና  ኤሽያ ዞኖች በሚያገኙት 100 ድምፅ የማሸነፍ እድላቸው ያመዝናል፡፡ ፕሬዝዳንት ሆኖ ለመመረጥ ቢያንስ ከ140 አገራት የድምፅ ድጋፍ መገኘት አለበት፡፡ በፕሬዝዳንትነት ምርጫው ከብላተር ጋር ለመፎካከር አመልክተው የነበሩት ሦስት ግለሰቦች ነበሩ፡፡ ታዋቂው እግር ኳስ ተጨዋች እና ፖርቱጋላዊው ሊውስ ፊጎ የመጀመርያው ነበር፡፡ ብዙም ወደ ምርጫ ዘመቻው ሳይገባ ፊፋ በአንድ ሰው አምባገንነት የሚመራ ተቋም ነው ብሎ በምሬት ራሱን አግልሏል፡፡ ሁለተኛው ደግሞ የሆላንድ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት ሲሆኑ የኤስያ እና የአፍሪካን ድጋፍ ማግኘት እንደሚከብድ ገልፀው ለድምፅ ፉክክር ሳይገቡ ቀርተዋል፡፡ ከሴፕ ብላተር ጋር ለመፎካከር የመጨረሻው እጩ ሆነው የቀሩት ግን የ39 ዓመቱ የጆርዳን ልዑል አልቢን ናቸው፡፡ ከአውሮፓ ዞን አገራት ከአሜሪካ እና ከሌሎች አገራት እስከ  50 ድምፅ ድጋፍ ማግኘት እንደሚችሉ ተገምተዋል፡፡  ሴፕ ብላተር በምርጫ አሸንፈው ፊፋን በ5ኛ የስራ ዘመን በፕሬዝዳንት መምራት ሲችሉ በአጠቃላይ 27 አመታት በስልጣኑ ይቆያሉ ማለት ነው፡፡

 በሙስና መረቡ ከሳሾችና ተከሳሾች

የፊፋ አመራሮች በቁጥጥር ስር ሲውሉ የስዊዘርላንድ መንግስት ከፍተኛ ሚና ነበረው፡፡ የአሜሪካ የአገር ውስጥ ደህንነት ቢሮ ሰባቱን ባለስልጣናት ዙሪክ በሚገኝ  ባለአምስት ኮከብ ሆቴል በቁጥጥር ስር አውሏቸዋል፡፡ በሰው 4ሺ ዶላር የሚከፈልበትና ከፍተኛ ድሎት ያለው ያለው ባወር የተባለ ሆቴል ነበር፡፡  ኤፍ ቢ አይ ያለፉት 24 ዓመታት በፊፋ እንቅስቃሴ ዙሪያ ምርመራ እና ክትትል ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ በዓለም ዋንጫ አዘጋጆች ምርጫ፣ በፊፋ የፕሬዝዳንትነት ሹመትና ከስፖንሰርሺፕ ውሎች በተገናኘ ብዙ ወንጀሎች ተፈጽመዋል በሚል መነሻ ነው፡፡ ከዚህ በተያያዘ 9 የእግር ኳስ አመራሮች እና አምስት የትልልቅ ስፖርት ሚዲያ እና ፕሮሞሽን ኩባንያ አመራሮች በሙስና መረብ መውተብተባቸውን ሲገለፅ ከ150 ሚሊዮን ዶላር መመዝበሩ ተረጋግጧል፡፡ በቁጥጥር ስር የዋሉት ሰባቱ የፊፋ አመራሮች ከላቲንና ከካራቢያን አገራት ውክልና አግኝተው ለፊፋ የሚሠሩ ናቸው፡፡ ከተከሳሾቹ መካከል ሁለቱ ብቻ ናቸው የአሜሪካ ዜግነት ያላቸው፡፡

14ቱ ፊፋ ባለስልጣናት  እና የማርኬቲንግ ወኪሎች በህገወጥ ድለላ፤ ሴራና ጉቦ  በአሜሪካ ፍትህ አስተዳደር በ47 ወንጀሎች ተከስሰዋል፡፡ በአለም አቀፍ እግር ኳስ ውድድሮች በማርኬቲንግ እና የሚዲያ መብት ለሚኖሩ ገቢዎች ሲባል ጉቦ የበዛባቸው ድርድሮች ተካሂደዋል ይባላል፡፡ከላይ የተጠቀሱት የውስጥ ወንጀሎች የአሜሪካ የፍትህ አስተዳደር ያቀረባቸው ክሶች ናቸው፡፡ ክስ በ2010 እኤአ ላይ ደቡብ አፍሪካ 19ኛውን ዓለም ዋንጣ ለማዘጋጀት በባልስልጣናቷ በኩል 10 ሚሊዮን ዶላር ጉቦ መክፈሏን የሚያረጋግጥ ማስረጃ አለኝ ብሎ ተጨማሪ ክስ የሚያቀርበው የአሜሪካ መንግስት በ2011 እኤአ ላይ ብላተር ለ4ኛ ጊዜ የፊፋ ፕሬዝዳንት ሆነው ሲመረጡ ድምፅ ለሰጧቸው አገራት በነፍስ ወከፍ እስከ 40ሺ ዶላር መክፈላቸውን እየገለፀም ነው፡፡

በሙስና ወንጀሎቹ ላይ የ24 ዓመታት ክትትል ማድረጉን ያሳወቀው የአሜሪካ የፍትህ አስተዳደር ሴፕ ብላተርን በክሱ ዝርዝር ባይጠቅስም አሜሪካ ቢገቡ ያስራቸዋል የሚል ዘገባ የተናፈሰ ቢሆንም ማረጋገጫ አልሰጠም፡፡ ብላተርም የክሱ አካል እንዳልሆኑ በልበ ሙሉነት ሲናገሩ ሌሎች ትልልቅ የፊፋ ባለስልጣናት ሊታሰሩ እንደሚችሉ እርግጠኛ ነኝ ብለዋል፡፡

ፊፋ ለዓመታዊ ደሞዝ እስከ 88 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጣ ሲሆን የስራ አስፈፃሚ አባል ለሆኑት 13 ባለስልጣናቱ እስከ 40 ሚሊዮን ዶላር መክፈሉ የሙስናው መገለጫ እንደሆነም የአሜሪካ ሚዲያዎች ይዘግባሉ፡፡

ሌላው ከሳሽ የስዊዘርላንድ መንግስት ሲሆን ክስ ያቀረበው ራሽያ እና ኳታር የዓለምዋንጫዎች አዘጋጆች ሆነው የተመረጡት በሴራ ተቀናብሮ እና ጉቦ ተሰጥቶ ነው ይላል፡፡

ባለፈው አመት በፊፋ ተቀጥሮ የነበረው ማይክል ጋርሺያ የተባለው የቀድሞ አቃቤ ህግ በሁለቱ አዘጋጆች አመራረጥ ዙርያ በ432 ገፆች የምርመራ ሪፖርት አቅርቦ ነበር፡፡

ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ይህ ሪፖርት ይፋ እንዳይሆን በማገዱ ከሃላፊነቱ ራሱን ማግለሉ አይዘነጋም፡፡

በተለይ በ2012 እ.ኤ.አ ራሺያ እንዲሁም በ2022 ኳታር 21ኛውና 22ኛውን የዓለም ዋንጫ እንዲያዘጋጁ የተመረጡት በሙስና በተደለሉ የፊፋ አመራሮችና ሌሎች ተቋማት የተቀናጀ የወንጀል መረብ ነው የሚል ውንጀላ ቀርቧል፡፡

የተበጠበጠው የስፖንሰርሺፕ ገበያ

የፊፋ ቀውስ ዓለም አቀፉን የእግር ኳስ የስፖንሰርሺፕ ገበያ የበጠበጠው ሲሆን አንዳንድ ትልልቅ ስፖንሰር አድራጊ ኩባንያዎች ከፊፋ ጋር የላቸውን ውል ለማውረስ እያጤኑ ናቸው ተብሏል፡፡

ፊፋ የገባበት የሙስና ቀውስ ከፍተኛ ገቢ የሚያስገኙለትን ትልልቅ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎችም እያስከፋ ነው፡፡ በተለይ ቪዛ ካርድ የተባለው ኩባንያ ፊፋ በአስተዳደሩ ላይ ስርነቀል ለውጥ ካላደረገ የውል ስምምነቱን ለማፍረስ እንደሚገደድ ገልጿል፡፡ የፊፋ አብይ ስፖንሰሮች ከሆኑት መካከል አዲዳስ፤ ኮካኮላ እና ሃዩንዳይም ሁኔታውን የሚያወግዝ መግለጫዎች አቅርበዋል፡፡

 እነዚህ ትልልቅ ኩባንያዎች በዓመት እስከ 28 ሚሊዮን ዶላር በነፍስ ወከፍ ለፊፋ በመክፈል እስከ የሚቀጥሉት ሁለት ዋንጫዎች በመስራት ለመቀጠል ይፈልጋሉ፡፡

አዲዳስ የሙስና ቀውሱ ወደየተባባሰ ሁኔታ እንዳያመራ በማለት ስጋቱን ሲገልፅ፤ ኮካኮላ በበኩሉ የዓለም ዋንጫን ገፅታ ጥላቻ የቀባ ክስተት ብሎ አውግዟል፡፡

ፊፋ የገቢውን 90 በመቶ ከዓለም ዋንጫ እንደሚያገኝ ይታወቃል፡፡ ብራዚል በ2014 እኤአ ላይ ያዘጋጀችው 20ኛው ዓለም ዋንጫ ላይ ፊፋ ያገኘው ንፁህ ትርፍ 2 ቢሊዮን ዶላር፡፡

ዓለምዋንጫው በተከናወነባቸው ከ2011 እስከ  2014 እኤአ  ባሉት አራት አመታት በሚዲያ እና የማርኬቲንግ መብት ገቢ የሆነው 6.4 ቢሊዮን ዶላር ነበር፡፡ ለዓለም ዋንጫ ትኬት በመሸጥ ያስገባው ደግሞ 527 ሚሊዮን ዶላር ነው፡፡ ከስፖንሰሮች ደግሞ 106 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ነበረው፡፡

 

 

 

ዛሬ ምሽት በአገራችን ያልተለመደ ልዩ የፋሽን ሐሳብ (አይዲያ) ብሥራተ ገብርኤል በሚገኘው ላፍቶ ሞል በታዳሚዎች እንደሚቀርብ ተገለፀ፡፡

ሁሉም ሰው የራሱ የአለባበስ ፋሽን ስላለው ፋሽን የሚለው ቃል ሁልጊዜ በሞዴሎች ብቻ መገለጽ የለበትም ያሉት የካይሙ ኢትዮጵያ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ተስፋ ገ/አብ፤ የዝግጅቱ ዓላማ የጋበዝናቸው እንግዶች ደስ የሚላቸውንና የራሳቸውን ፋሽን ይዘው መጥተው ፍላጎታቸውን ነፃ ሆነው እንዲናገሩ ነው ብለዋል፡፡

አቶ ተስፋ ትናንት በጽ/ቤታቸው ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ አንዲት ሴት በአገራችን ባህል እብድ ናት እንዴ? በሚያሰኝ የሚያስገርምና የሚያስቅ ሁኔታ፣ “እኔ በጣም አጭርና ጥብቅ ያለ ሚኒስከርት መልበስ በጣም ያስደስተኛል” የሚል ሀሳብ ብታቀርብ መብቷ እንደሆነ ገልጸው፣ የተለያዩ ሰዎች ከእሷ የባሰ አስገራሚ የፋሽን ሐሳብ ሊያቀርቡ እንደሚችሉ ጠቁመዋል፡፡ ካይሙ ኢትዮጵያ፣ በቅርቡ ማንኛውንም ቁሳቁስ (የፋሽን አልባሳት፣ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች፣ መጻሕፍት፣ ምግብና መጠጦች፣ የስፖርት፣ የቤትና የቢሮ ዕቃዎች ወዘተ) በኢንተርኔት በተመጣጣኝ ዋጋ የሚሸጥና ደንበኛው የገዛውን ዕቃ በአድራሻው የሚያስረክብ ድርጅት መሆኑን የጠቀሱት ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ፤ የዝግጅቱ ሌላው ዓላማ ካይሙን ከፋሽን ጋር በማያያዝ ማስተዋወቅ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

ከምሽቱ 3፡00 እስከ ሌሊቱ 7፡00 የሚቆየውን የፋሽን አይዲያ (ሃሳብ) ፕሮግራም ያዘጋጁት ካይሙ ኢትዮጵያ ከኢጋኖፍ ቮድካ ጋር በመተባበር ሲሆን፣ በዝግጅቱ የተለያየ ጣዕም ያላቸው ቮድካና ሌሎች መጠጦች እንደሚቀርቡ፣ 4 ዲጄዎች (ሁለት ከውጭ፣ ሁለት ከአገር ውስጥ) ሙዚቃዎቻቸውን በማቅረብ ታዳሚውን እንደሚያዝናኑ፣ በዲዛይን ሥራቸው ታዋቂ የሆኑት አና ጌታሁን፣ አቡጊዳና አዶት ዲዛይነሮች፣ የሠሩትን አልባሳት ሞዴሎችን በማልበስ እንደሚያቀርቡና የዕለቱ ዝግጅት በኤፍ.ኤም 97.1 “ራዲዮ ሄሎ ሌዲስ” በተባለ ፕሮግራም ከ6-7 ሰዓት እንደሚተላለፍ አቶ ተስፋ ገ/አብ አስታውቀዋል፡፡

 

 

 

 

        በ2003 በከፍተኛ ሙቀት ከ3ሺህ በላይ ሰዎች ሞተዋል

     በህንድ ሰሜናዊና ማዕከላዊ አካባቢዎች የተከሰተውን ያልተለመደ ሃይለኛ ሙቀት መቋቋም አቅቷቸው በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ለሞት የተዳረጉ ሰዎች ቁጥር ከ1ሺህ በላይ መድረሱን ኢንተርናሽናል ቢዝነስ ታይምስ ዘገበ፡በያዝነው ሳምንት በተጠቀሱት አካባቢዎች የሙቀት መጠኑ እስከ 50 ዲግሪ ሴንቲግሬድ መድረሱን የጠቆመው ዘገባው፤ የአገሪቱ የሜቲዮሮሎጂ ባለስልጣንም የሙቀት መጠኑ መጨመር በታየባቸው የአገሪቱ ግዛቶች የከፋ ጥፋት ሊከሰት እንደሚችል ማስጠንቀቁን ገልጿል፡፡በአብዛኞቹ የህንድ ግዛቶች የሳምንቱ አማካይ የሙቀት መጠን 45 ዲግሪ ሴንቲግሬድ መድረሱ የተገለጸ ሲሆን፣ የሙቀት መጠኑ በከፍተኛ ሁኔታ መጨመር የሰዎችን ተፈጥሯዊ አደጋን የመከላከል የሰውነት ስርዓት እንደሚያዛባና ለድካምና ለሞት እንደሚዳርግ ሃኪሞች መናገራቸውን ዘገባው አብራርቷል፡፡

የአገሪቱ መንግስት ዜጎች በከፍተኛው ሙቀት እንዳይጠቁ ለመከላከል የተለያዩ እርምጃዎችን እየወሰደ ሲሆን፣ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የማቀዝቀዣ ውሃና ድርቀትን የመከላከያ ፈሳሾች እየተሰራጩ ነው ብሏል፡፡ ለሞት የተዳረጉት ሙሉ በሙሉ ለማለት በሚቻል መልኩ አረጋውያን እንደሆኑም ታውቋል፡፡ላልተለመደው የሙቀት መጨመር የተለያዩ ምክንያቶች እየተሰጡ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል ከፓኪስታን አቅጣጫ ወደ ህንድ የሚነፍሰው ሞቃት ንፋስ እንደሚገኝበት ዘገባው ጠቁሟል፡፡ህንድ በእነዚህ ወራት ሞቃት አየር እንደሚኖራት ቢታወቅም የዘንድሮው ሙቀት ግን ከተለመደው በ6 ዲግሪ ሴልሺየስ እንደሚበልጥ የዘገበው ኢንዲያን ኤክስፕረስ ጋዜጣ፣ አንድራ ፕራዴሽ በተባለችው የህንድ ግዛት ባለፈው እሁድ የተመዘገበው 48 ዲግሪ ሴንቲግሬድ ሙቀት ባለፉት 68 አመታት በግዛቲቱ ታይቶ የማይታወቅ እንደሆነ ገልጿል፡፡

የህንድ የሳይንስ ኢንስቲቲዩት ጥናት እንደሚለው፤ ባለፉት 15 አመታት ከሙቀት መጨመር ጋር በቀጥታ በተያያዘ ሰበብ፤ በአገሪቱ በየአመቱ ለህልፈተ ህይወት የሚዳረጉ ሰዎች አማካይ ቁጥር 153 የነበረ ቢሆንም፣ በጊዜ ሂደት ግን ቁጥሩ እየጨመረ መጥቷል ተብሏል፡፡

ከአምስት አመታት በፊት አህመዳባድ በተባለው የህንድ አካባቢ የተከሰተውና 112 ዲግሪ ፋራናይት የተመዘገበው ከፍተኛ የሙቀት መጠን 1ሺህ 300 ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት መዳረጉን ያስታወሰው ዋሽንግተን ፖስት በበኩሉ፣ እ.ኤ.አ በ2003 በአንድራ ፕራዴሽ ግዛት የተከሰተ ከፍተኛ ሙቀትም ከ3ሺህ በላይ ሰዎችን መግደሉን አክሎ ገልጿል፡፡

የሙቀት መጠኑ እስከ ወሩ መጨረሻ ይቀጥላል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፣ የህንድ የሜቲዮሮሎጂ ባለስልጣን ሃላፊ ዴቬንድራ ሻርማም፤ ዜጎች ከቤታቸው እንዳይወጡና ብዙ ውሃ እንዲጠጡ ጥሪ ማቅረባቸውንና በሙቀት መጠኑ መጨመር የተነሳ በአገሪቱ ያለው አጠቃላይ እንቅስቃሴ መስተጓጐሉን ጠቁሟል፡፡

 

 

 

Published in ከአለም ዙሪያ

 

 

 

    በሽልማት ገንዘብ ፤ በቴሌቭዥን ስርጭት ፤ በስፖንሰርሺፕና ተያያዥ ንግዶች

    የ2007 የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ነገ ፍፃሜውን ያገኛል፡፡ ቅ/ጊዮርጊስ ሻምፒዮን መሆኑን ያረጋገጠው ከሳምንት በፊት ነበር፡፡

የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ በአዲስ መዋቅር መካሄድ ከጀመረ ወዲህ ቅ/ጊዮርጊስ ለ12ኛ ጊዜ የሻምፒዮናነት ክብሩን መጐናፀፉ ይሆናል፡፡ ከነገው የሊጉ የመጨረሻ ጨዋታ በፊት ጊዮርጊስ በ25 ጨዋታዎች 54 ነጥብ እና 23 የግብ ክፍያ አስመዝግቧል፡፡  የሊጉን ሻምፒዮናት ያረጋገጠው ግን 15 ጨዋታዎችን ድል በማድረግ፤ በ6 አቻ በመውጣት እና በ3 በመሸነፍ ከሳምንት በፊት ነበር፡፡ አዳማ ከነማ በ42 ነጥብ ደደቢት በ41 ነጥብ ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለፕሪሚዬር ሊጉ ሻምፒዮን እንዲሁም በተለያዩ ደረጃዎች የውድድር ዘመኑን ለጨረሱ ክለቦች እና ኮከብ ተጨዋቾች ምን ያህል የገንዘብ ሽልማት እንደሚሰጥ አይታወቅም፡፡ ሻምፒዮኑ ክለብ ቅ/ጊዮርጊስ ከሚያገኘው የዋንጫ ሽልማት ባሻገር ከ80-100 ሺ ብር ይሸለማል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን ለኮከብ ተጨዋቾች እስከ 50ሺ ብር ሊበረከት ይችላል፡፡

የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ከመቼውም ጊዜ ለተለየ ሁኔታ በዘንድሮው የውድድር ዘመን ለተለያዩ ዘርፎች ኮከቦች ሆነው ለሚመረጡ ተጨዋቾች ልዩ የመመዘኛ መስፈርት ማውጣቱም ታውቋል፡፡ መሠረት መገናኛ ብዙሐናትና አሰልጣኞች በሚሰጡት ድምፅ መሠረት የዓመቱ የሊጉ ኮከብ ተጨዋች፣ ኮከብ ግብ ጠባቂ እና የስፖርታዊ ጨዋነት ተሸላሚ ተለይተው ይታወቃሉ፡፡ የሊጉን የኮከብ ግብ አግቢነት ፉክክር የደደቢት ተጨዋች የሆነው ናይጄሪያዊው ሳሙኤል ሳኑሚ በ22 ጐሎች እየመራ ነው፡፡  ሳኑሚ የዮርዳኖስ አባይን 14 አመት የቆየ የ24 ግብ በአንድ የውድድር ዘመን የማስቆጠር ሪኮርድ ለመስበር ነገ በመጨረሻው ሳምንት ከቀድሞ ክለቡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር በሚደረገው ጨዋታ ላይ ሌላ ሐት-ትሪክ መስራት ይጠበቅበታል፡፡

ዘንድሮ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ በጊዜ መጠናቀቁ የተለየ ያደርገዋል፡፡  አሠልጣኝ ያሰናበቱት የፕሪሚየር ሊጉ ክለቦች  ሰባት መሆናቸው ደግሞ ሌላው መግለጫ ነው፡፡  ወልዲያ ከነማ፣ ሐዋሳ ከነማ፣ ደደቢት፣ አርባ ምንጭ ከነማ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ኢትዮጵያ ቡናና ዳሽን ቢራ አሰልጣኞቻቸውን በማባረር የውድድር ዘመኑን የጨረሱ ናቸው፡፡

 ከፕሪሚዬር ሊጉ የወረደው ክለብ ደግሞ  አንዱ ወልደያ ከነማ ሲሆን ሌላኛው ዛሬ ነገ በሚደረጉት የመጨረሻ ሳምንት ጨዋታዎች ይታወቃል፡፡

በአዲስ መዋቅር መመራት ከጀመረ ዘንድሮ 17ኛ ዓመት የውድድር ዘመኑን የያዘው የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ በአገር ውስጥ የህትመትና የብሮድካስት ሚዲያዎች እንዲሁም በድረገፆች ከፍተኛ ሽፋን እያገኘ ነው፡፡ በገቢ አቅሙ ግን አላደገም፡፡ በውድድር ዘመኑ መጨረሻ ክለቦች ከተለያዩ ንግዶች የስፖንሰርሺፕ ገቢዎች እና ከሽልማት ገንዘብ ተጠቃሚ አይደሉም፡፡ ለቀጣይ የውድድር ዘመን ይህን ለመለወጥ መሠራት ይኖርበታል፡፡

የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ በ2008 ዓ.ም የውድድር ዘመን የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ አብይ ስፖንሰር አግኝቶ በውድድር ዘመኑ መግቢያ ዳጐስ ያለ የገንዘብ ሽልማት ሊያበረክትላቸው ይጠበቃል፡፡ የተመረጡ የፕሪሚዬር ሊጉ ጨዋታዎች በቀጥታ የቴሌቭዥን ስርጭት ሽፋን የሚያገኙበት ዕድልም መፈጠር አለበት፡፡ ለሊጉ አብይ የስፖንሰር ሺፕ ውል በማግኘት ውድድሩን ለማንቀሳቀስ በጥናት ላይ የተመሠረተ ርምጃ መፈጠር አለበት፡፡ የፕሪሚዬር ሊጉ ክለቦች የትልልቅ ኩባንያዎችን፣ ባለሀብቶችና፣ የደጋፊዎችን ትኩረት የሚስቡበትን አሰራር በመፍጠር የገቢ አቅማቸውን ለማጠናከር መስራት አለባቸው፡፡

በየውድድር ዘመኑ የሊጉ ፉክክርና የክለቦች ደረጃ ጠቡ ተጠናክሮ መቀጠሉ የአገሪቱን እግር ኳስ ያግዛል፡፡ በተለያዩ አህጉራዊ ውድድሮች ክለቦች የሚኖራቸውን ተፎካካሪነት ያሳድጋል፡፡ የሊጉ በገቢ አቅም መጠናከር የብሔራዊ ቡደኑንም ውጤታማነት የሚደግፍ መሆኑም መታወቅ አለበት፡፡

ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን፣ ለፕሪሚዬር ሊግ ተወዳዳሪ ክለቦች፣ ደጋፊዎቻቸውና አመራራቸው መነቃቃት ይፈጥራል በሚል ለአፍሪካ ደረጃ ከፍተኛ ስኬት እያገኘ ያለውን የደቡብ አፍሪካ የኮከቦች ሊግ ስፖርት አድማስ በአጭሩ ለመዳሰስ ሞክሯል፡፡

የደቡብ አፍሪካ ሊግ ከ2 ሳምንት በፊት የተገባደደ ሲሆን በታሪኩ ለ4ኛ ጊዜ የሻምፒዮናነት ክብሩን በመቀዳጀት ካይዘርቺፍ ተሳክቶለታል፡፡ የደቡብ አፍሪካ ሊግ በምርጥ የውድድር ሂደቱ፤ በገቢው ጠንካራነት፤ በቴሌቭዥን ስርጭት ፤ በስታድዬም ተመልካች ብዛት እና ከደጋፊዎች ጋር ባለው መጠነ ሰፊ ትስስር እንደምሳሌ እንደሚጠቀስ  ቬንቹር አፍሪካ የተባለ ድረገፅ በሰራው ትንተና ተመልክቷል፡፡ ከደቡብ አፍሪካ ሊግ ባሻገር በስኬታማ የውድድር ሂደቱ፤ በተመልካቹ ብዛት እና በገቢ አመንጭነቱ ተቀራራቢ ስኬት ያላቸው ሊጐች በአልጄርያ እና በሞሮኮ የሚገኙት ናቸው፡፡ የግብፅ እና የቱኒዝያ ሊጎች ካለፉት አምስት አመታት በስታድዬሞች ስርዓት አልበኝነቱ በመብዛቱ አሽቆልቁለዋል፡፡ የናይጄርያው ሊግ ደግሞ በአስተዳደር ችግሮች፤ በዳኝነት ድክመቶች እና በተለያዩ ውዝግቦች በምሳሌነት የሚጠቀስ አይደለም፡፡

የገቢ ምንጮች

በደቡብ አፍሪካ እንደሚካሄዱ ብዙ የስፖርት እንቅስቃሴዎች የእግር ኳስ ሊጉ በገቢ አመለጭነት ብዙ ርቀት ተጉዟል፡፡ ሊጉ “አብሳ” በተባለ የአገሪቱ ትልቅ ባንክ በኦፊሴላዊ ስፖንሰርነት የሚደገፍ ሲሆን ከስሩ ያሉ ውድድሮች እና የጥሎ ማለፍ ሻምፒዮናው በኮርፖሬት ስፖንሰርሺፕ እና በአጋርነት “ኔድ ባንክ” እና “ኤምቲኤን” ከተባሉ የፋይናንስ ተቋማት ጋር በፈፀሙት ውል ይከናወናሉ፡፡ እነዚህ ስፖንሰሮች ከደቡብ አፍሪካ የእግር ኳስ ውድድሮች ጋር ለመስራት ፍላጎት ያደረባቸው በሚያገኙት የብራንድ ግንባታ ተጠቃሚ በመሆናቸው ነው፡፡ በሊጉ የሚወዳደሩ ክለቦችን ደጋፊዎቻቸውን በልዩ ፍቅር እና ትኩረት ስታድዬም በመግባት እና በቲቪ ስርጭት መከታተላቸው አንዱ ውጤት ነው፡፡ የሊጉ ሻምፒዮን አሁን ባለፈው ሰሞን የውድድር ዘመኑን በድል ያጠናቀቀው ካይዘር ቺፍ ያገኘው ሽልማት 836ሺ ዶላር ነው፡፡ የናይጄርያው የዘንድሮ ሻምፒዮን ያገኘው 86ሺ ዶላር ብቻ ነው፡፡

የደጋፊ ሃይል የደቡብ አፍሪካ እግር ኳስ የደጋፊዎችን ትኩረት እና ፍላጎት በማግኘት በአፍሪካ የሚስተካከለው የለም፡፡ ስታድዬሞች ከስርዓት አልበኝነት በተያዙ ችግሮች አለመረበሻቸው እንዱ የደጋፊዎችን ትኩረት ያመጣ ነው፡፡ ሊጉ በቲቪ ስርጭት በማላው ዓለም እስከ 86 ሚሊዮን ቋሚ ተከታታይ ለማፍራት መቻሉም ሌላው የስኬቱ ምስጥር ነው፡፡ብቁ የውድድር አመራር በናይጄርያ የውድድር መርሃ ግብሮች መዛባት፤ በሌሎች የአፍሪካ ክፍሎች በዳኝነት ብቃት መዳከም፤ በሰሜን አፍሪካ ስታድዬሞች ያሉ ስርዓት አልበኝነቶች በደቡብ አፍሪካ ሊግ ያጋጥማሉ ተብሎ አይታሰብም፡፡ ለዚህ ዋና ምክንያቱ የሊጉ አስተዳዳሪዎች ውድድሮቹን በብቃት የሚመሩበት ሂደት ነው፡፡የሊጉ አስተዳዳሪዎች ግጥሚያዎች በስታድዬም ሲካሄድ አስፈላጊውን አስተማማኝ የደህንነት ጥበቃ በማድረግ ተመጣጣኝ የስታድዬም ትኬት በማሰራጨት፤ በተሟላ የፕሮፌሽናል መንገዶች ስርጭት እንዲኖራቸው በማስቻል ብበቃት ሃላፊነታቸውን መወጣታቸውም ሌላው ውጤት ነው፡፡

 

 

 

 

 

 

 

      በ2000 የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች 400 ሚ. ብቻ ነበሩ

    የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አለማቀፉ የቴሌኮሙኒኬሽን ህብረት፤ ከዓለማችን ህዝብ ግማሽ ያህሉ እስከያዝነው የፈረንጆች 2015 አመት መጨረሻ የኢንተርኔት ተጠቃሚ ይሆናል ተብሎ እንደሚጠበቅ ማስታወቁን ቢቢሲ ዘገበ፡ህብረቱ ባለፈው ማክሰኞ ባወጣው ሪፖርት እንዳለው፤ እስከ መጪው ታህሳስ ወር ድረስ በአለማችን የኢንተርኔት ተጠቃሚ የሆኑ ሰዎች አጠቃላይ ቁጥር 3.2 ቢሊዮን እንደሚደርስና ከዚህ ውስጥም 2 ቢሊዮን ያህሉ ያደጉ አገራት ዜጎች እንደሚሆኑ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

የሞባይል ብሮድባንድ አገልግሎት መስፋፋቱ በአብዛኞቹ የአለማችን አገራት የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ቁጥር ለማደጉ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል ያለው ሪፖርቱ፣ በአሁኑ ወቅት በኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ብዛት ቻይና፣ አሜሪካና ህንድ መሪነቱን ይዘው እንደሚገኙና በአመቱ መጨረሻ ግን ህንድ ሁለተኛ ትሆናለች ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጿል፡፡

የአለማችን ህዝብ የኢንተርኔት ተጠቃሚነት ባለፉት 15 አመታት ከ6.5 በመቶ ወደ 43 በመቶ ማደጉን ያመለከተው ሪፖርቱ፤ በቤታቸው የኢንተርኔት አቅርቦት ያላቸው ሰዎች ቁጥርም በ2005 ከነበረበት 18 በመቶ፣ ዘንድሮ 46 በመቶ ደርሷል ብሏል፡፡

እ.ኤ.አ በ2000 በአለማችን የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ቁጥር 400 ሚሊዮን ብቻ እንደነበር ያስታወሰው ሪፖርቱ፣ በአሁኑ ወቅት የአለማችን 69 በመቶ የሚሆነው አካባቢ የ3ጂ ኢንተርኔት ተጠቃሚ መሆኑን ጠቁሞ፣ ይሄም ሆኖ ግን 29 በመቶ የሚሆኑ የገጠር አካባቢዎች ብቻ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጿል፡፡በሞባይል ብሮድባንድ ሽፋን ከአለማችን ዝቅተኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው አፍሪካ ስትሆን፣ በዘርፉ አህጉሪቱ ያላት ሽፋን 17.4 በመቶ ብቻ ነው ብሏል ሪፖርቱ፡፡

 

 

 

 

Published in ከአለም ዙሪያ
Page 2 of 19