የፊልሙ ታሪክ መቋጫ ገና አልተወሰነም
“ጠመንጃ ምናምን አናሳይም፤ ዩፎዎችንም አናስገባም” - (የፊልሙ ዳይሬክተር ሩፒሽ ፖል)

ከወራት በፊት 239 ሰዎችን አሳፍሮ በበረራ ቁጥር ኤም ኤች 370 ከኳላላምፑር በመነሳት ወደ ቢጂንግ ጉዞ ከጀመረ በኋላ፣ ድንገት ደብዛው ጠፍቶ በቀረውና በአለማችን የበረራ ታሪክ በአሳዛኝነቱና በእንቆቅልሽነቱ በሚጠቀሰው የማሌዢያ አየር መንገድ ቦይንግ 777 አውሮፕላን ዙሪያ የሚያጠነጥነውና በህንዳዊው ዳሬክተር ሩፒሽ ፖል አዘጋጅነት የሚሰራው ፊልም እያወዛገበ መሆኑን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተውንና አስፈሪ (ትሪለር) ዘውግ ያለውን ይህን ፊልም፣ በ35 ቀናት ጊዜ ውስጥ በህንድና በአሜሪካ የተለያዩ አካባቢዎች ቀርጾ ለመጨረስ መታቀዱን የዘገበው ቢቢሲ፣ እውነተኛው አውሮፕላን የደረሰበት ባልታወቀበትና ፍለጋው ሙሉ ለሙሉ ባልተጠናቀቀበት ሁኔታ፣ ፊልሙ ለእይታ መብቃቱን ብዙዎች እንዳልወደዱትና ፊልሙ ገና ከወዲሁ ውዝግብ መፍጠሩን አመልክቷል፡፡
ዳይሬክተሩ ሩፒሽ ፖል፤ ከሳምንት በፊት በተከናወነው የኬንስ ፊልም ፌስቲቫል ላይ እንደተናገረው፣ “ዘ ቫኒሺንግ አክት” የሚል ርዕስ በተሰጠውና 3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዶላር ይፈጃል ተብሎ በተገመተው በዚህ ፊልም ላይ ከ200 በላይ ተዋንያን ይሳተፉበታል፡፡
90 ደቂቃ ርዝማኔ የሚኖረው “ዘ ቫኒሺንግ አክት” ፣ በአውሮፕላኑ ተሳፋሪዎች ቤተሰቦች ላይ ምንም አይነት አሉታዊ ተጽዕኖ እንደማይፈጥር የተናገሩት ዳይሬክተሩ፤ ክስተቱን ተጣድፈው ለገንዘብ ማግኛ የመጠቀም ፍላጎት እንደሌላቸው ገልጸዋል፡፡
ዳይሬክተሩ በአውሮፕላኑ ዙሪያ ፊልም እየሰሩ እንደሚገኙ መግለጻቸውን ተከትሎ ከየአቅጣጫው የሚሰነዘርባቸውን ትችት እያጣጣሉ እንደሆነ፣ ዘ ጋርዲያንን ጨምሮ በርካታ አለማቀፍ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል፡፡
“የአውሮፕላኑ ደብዛ ጠፍቶ መቅረትና በየአቅጣጫው ሲካሄድ የቆየው ፍለጋ ዛሬም ድረስ ምንም አይነት ተጨባጭ ውጤት አለማስገኘቱ፣ በአለምአቀፍ ደረጃ የፈጠረው ውዝግብ፣ በተዘዋዋሪ መንገድ የፊልሙን ተፈላጊነት የሚጨምረው ቢሆንም፤ የኛ አላማ ግን፣ ከዚህ አሳዛኝ የበረራ ታሪክ ገንዘብ ማካበት አይደለም” ብለዋል ፖል፤ ለሆሊውድ ሪፖርተር፡፡
“ፊልሙ በከፊል የፈጠራ ስራ ነው፡፡ ቢሆንም ግን በአውሮፕላኑ ነጥፋት ዙሪያ ሲ ኤን ኤንን ጨምሮ አንዳንድ መገናኛ ብዙሃንና ግለሰቦች የሰጡትን መላምት እንደ ግብዓት ተጠቅመናል፡፡ የፊልሙ ዘውግ አስፈሪ ቢሆንም፣ አንዳንዶች በአውሮፕላኑ መጥፋት ዙሪያ የሚሰጡትን አጉል መላምት መሰረት አድርገን በፊልሙ ውስጥ አንዳንድ ዝባዝንኬዎችን አናካትትም፡፡ ጠመንጃ ምናምን አናሳይም፤ ዩፎዎችንም አናስገባም፡፡ ታሪኩ ደግሞ የአምስት ወጣት ጓደኛሞችን የበቀል እቅድና አለምን ቀውስ ውስጥ በሚከት መጨረሻቸው ዙሪያ የሚያጠነጥን ነው፡፡ እርግጥ የታሪኩ መጨረሻ ምን መምሰል አለበት የሚለውን አሳሳቢ ጉዳይ በተመለከተ፣ ገና አሁንም ድረስ ይህ ነው የሚባል ውሳኔ ላይ አልደረስኩም” ሲሉም አክለዋል፡፡
የፊልሙን ፕሮጀክት በተመለከተ ነቀፌታ የበዛባቸው ተባባሪ ዳይሬክተሩ ስሪታማ ዱታ በበኩላቸው፣ ይሄ ሁሉ ውግዘት አግባብ አለመሆኑን ገልጸው፣ በእውነተኛው አውሮፕላንና በፊልሙ አውሮፕላን መካከል ያለው ግንኙነትና መመሳሰል፣ ሁለቱም መጥፋታቸው ብቻ ነው ሲሉ ጉዳዩን አስተባብለዋል፡፡ ፊልሙን ፕሮዲዩስ ለማድረግ፣ ከእስያ ሃገራት  በተለይ ደግሞ ከጉዳዩ ዋነኛ ባለቤቶች ከማሌዢያና ከቻይና ኩባንያዎች ዘንድ ከፍተኛ ፍላጎት እየታየ እንደሚገኝ የተናገሩት ፖል፤ እስከ መጪው መስከረም ወር አጋማሽ ድረስ አጠቃላይ ስራው ተጠናቆ በአለም አቀፍ ደረጃ ለእይታ እንደሚበቃ ገልጸዋል፡፡
ዳይሬክተሩ ለሙከራ ብለው የቀረጹትና በኬንስ ፌስቲቫል ላይ ለእይታ ያቀረቡት የደቂቃዎች ርዝማኔ ያለው የፊልሙ ክፍል፣ በአንዲት የአውሮፕላኑ ሰራተኛና በአንድ ሽጉጥ የያዘ ተሳፋሪ መካከል የፍቅር ግንኙነት እንደነበር የሚያመላክት ትዕይንት የያዘ ነበር፡፡ ይህ አጭር ትዕይንት በዩቲዩብ ድረ-ገጽ ተለቆ 140 ሺህ ተመልካቾች ያዩት ሲሆን፣ አንዳንዶች ነቀፌታቸውን በመግለጽ ዳሬክተሩን “እብድ!”፣ “ክብር የሌለው!” እና “ጨካኝ!” ሲሉ ነቅፈውታል፡፡
በሚሰሯቸው ወሲብ ነክ ፊልሞች አነጋጋሪ ሆነው እንደዘለቁ የሚነገርላቸው ዳይሬክተሩ፤ የመጀመሪያ ስራቸው የሆነውን ‘ዘ ቴምፕቴሽንስ ቢትዊን ማይ ሌግስ’ ጨምሮ፤ ‘ካማሱትራ’ (በስሪ ዲ የተሰራ) እንዲሁም ‘ሞኖሎግስ ኦፍ ኤ ሴክስ ማኒክ’፣ ‘ዘ ሴክሬት ዲያሪስ ኦፍ ሞናሊዛ’ እና ሌሎች ፊልሞችን አዘጋጅተዋል፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 24 May 2014 15:00

የፀሐፍት ጥግ

አንድ ፅሁፍ ያለልፋት በቀላሉ ከተነበበ፣ ሲፃፍ በእጅጉ ተለፍቶበታል ማለት ነው፡፡
ኤንሪክ ጃርዴይል ፓንሴላ
እውነተኛ ፀሐፍትን ተስፋ ማስቆረጥ አይቻልም፡፡ ምንም ብትሏቸው ደንታ  ሳይሰጣቸው ይፅፋሉ፡፡
ሲንክሌይር ልዊስ
በእጄ ላይ ብዕር ይዤ እንቅልፍ ከጣለኝ ብዕሬን አትንኩብኝ፣ በእንቅልፍ ልቤ ልፅፍ እችላለሁ፡፡
ቴሪ ጉሌሜትስ
የመፃፍ ተሰጥኦ እንደሌለኝ ለማወቅ አሥራ አምስት ዓመት ፈጅቶብኛል፡፡ ፅሁፍን ማቆም ግን አልቻልኩም፡፡
 ምክንያቱም ያኔ  ዝነኛ ፀሃፊ ሆኛለሁ፡፡
ሮበርት ቤንችሌይ
የምንፅፈው አሁናችንን በኋላ ለማስታወስ ነው፡፡
 ቴሪ ጉሌሜትስ
ማንም ሰው  የፃፈውን ነገር ለሴት ሳያነብ መፅሃፍ ማሳተም የለበትም፡፡
ቫን ዊክስ ብሩክ
ሃኪሜ የምትኖረው ለስድስት ደቂቃ ብቻ ነው ቢለኝ በፍርሃት አልርድም፤ ፍጥነቴን
 ጨመር አድርጌ እፅፋለሁ እንጂ፡፡
አይሳክ አሲሞቭ

Published in የግጥም ጥግ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ለመጀመሪያ ጊዜ የእያንዳንዱን ክልል የጋብቻ ስነ - ስርዓትና ትውፊታዊ ክንውን ሰንዶ ሊያስቀምጥ እንደሆነ አስታወቀ፡፡ በዚህም መሰረት ሰኔ 2 ቀን 2006 ዓ.ም እያንዳንዱ ክልል፣ ክልሉን ይወክላሉ ያላቸውን የጋብቻ ሥርዓቶች ይዞ በመቅረብ ለሌላው ህብረተሰብ ያስተዋውቃል ተብሏል፡፡ የጋብቻ ስነ ስርዓቱና ትውፊታዊ ክንውኑ በመገናኛ ብዙሃን የሚሰራጭ ሲሆን ከዚያም በብሔራዊ ቴአትር ተሰንዶ ይቀመጣል ተብሏል፡፡ በዚህ ዝግጅት ላይ ሁሉም ክልሎች ተወክለው ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር በላከው መግለጫ አስታውቋል።

ዊሊያም ዎርድስዎርዝ (1770-1850)
እንግሊዛዊው ገጣሚ ዎርድስዎርዝ  ገና 15 ዓመት ሳይሞላው ነበር ወላጆቹን በሞት ያጣው፡፡ እንዲያም ሆኖ በእንግሊዝ የተሳካላቸውና ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሚባሉት ገጣምያን ተርታ ከመሰለፍ ያገደው ነገር አልነበረም፡፡ ግጥሞችን መፃፍ የጀመረው ገና ተማሪ ሳለ ቢሆንም 23 ዓመት እስኪሞላው ድረስ ግን አንድም የግጥም ሥራው አልታተመለትም ነበር። ዎርድስዎርዝ  የፃፋቸውን ግጥሞች የሚያነበው ለውሻው ሲሆን  ውሻው በተነበበለት ነገር ከጮኸ ወይም ከተበሳጨ፣ ዎርድስዎርዝ ግጥሙን ማሻሻልና እንደገና መፃፍ እንዳለበት ተገንዝቦ ወደ ሥራው ይገባል፡፡
ዲክ ኪንግ-ስሚዝ (1922-2011) በእንስሳት ላይ የተመሰረቱ የህፃናት መፃህፍትን በመፃፍ ይታወቅ የነበረው እንግሊዛዊው ደራሲ ዲክ ኪንግ- ስሚዝ፤በሙያ ዘመኑ ከ100 በላይ መፃህፍትን ፅፏል፡፡ ዝናን ያጎናፀፈው መፅሃፉ The Sheep Pig የተሰኘው ሲሆን ይሄ ሥራው Babe በሚል ርዕስ ወደ ፊልም ተቀይሮለታል፡፡ የመጨረሻ መፅሃፉ በ2007 እ.ኤ.አ የታተመለት ሲሆን The Mouse Family Robinson ይሰኛል፡፡ ደራሲው የፃፋቸው ታሪኮች አሁንም ድረስ በመላው ዓለም በሚገኙ ህፃናት ዘንድ በፍቅር እንደሚነበብለት ይነገራል፡፡


ከ800 ሚሊዮን በላይ መፃሕፍቶችን የቸበቸበችው የረዥም ልብወለድ ፀሐፊዋ ዳንኤላ ስቲል፤ የመጀመርያ ረቂቅ ፅሁፏን እስክታጠናቅቅ ድረስ በጥንት የትየባ ማሽን ላይ በቀን ለ20 ሰዓታት ትፅፋለች፡፡ በአንድ መፅሃፍ ላይ አተኩሮ ከመስራት ይልቅ በአንድ ጊዜ ከ4-5 የሚደርሱ መፃሕፍት ላይ በመስራትም ትታወቃለች፡፡
ጥቂት የማይባሉ የደራሲዋ ልብወለዶች ወደ አማርኛ ተተርጉመው ለአገራችን አንባቢያን መቅረባቸው የሚታወቅ ሲሆን ወደ ፊልም የተቀየሩ ሥራዎቿም በቅዳሜ የታላቅ ፊልም ፕሮግራም ላይ ለተመልካች  ይቀርቡ ነበር፡፡


ስቲፈን ኪንግ
ከ350 ሚሊዮን በላይ ኮፒዎች የተሸጡለት ይሄ አሜሪካዊ ደራሲ፤ ምንም ሳያስተጓጉል በየቀኑ ስድስት ገፆች ገደማ  ይፅፋል፡፡ በቀን ከ4 እስከ 6 ሰዓታት ማንበብና መፃፍ የማይችል ሰው ታላቅ ፀሐፊ የመሆን ህልሙን ይርሳው ሲልም ደራሲው ያስጠነቅቃል፡፡  
የድርሰት ትምህርት አንድን ሰው የመፃፍ ክህሎት ያስታጥቀዋል ብሎ የማያምነው ስቲፈን ኪንግ፤ ደራሲነት ከተፈጥሮ የሚገኝ ፀጋ ነው ባይ ነው፡፡ የመጀመርያ ድርሰቱን በ7 ዓመት እድሜው የፃፈው ኪንግ፤ ይሄን ድርሰት በ18 ዓመቱ ለአንድ መፅሄት እንደሸጠው ተዘግቧል፡፡ Carrie የተሰኘውን የመጀመርያ ልብወለዱን ከፃፈ በኋላ በተወዳጅ አስፈሪ (horror) ልብወለዶቹ እየታወቀ የመጣ ሲሆን የመጀመርያ አስፈሪ መፅሃፉም The Shining ይሰኛል፡፡  

አሜሪካዊው የልብ አንጠልጣይ ረዥም ልብወለዶች ደራሲ ዳን ብራውን፤ በሳምንት ለ7 ቀናት ሳያሰልስ በመፃፍ ይታወቃል - ከሌሊቱ 10 ሰዓት ጀምሮ፡፡  ይሄ የቀድሞ የእንግሊዝኛ መምህር፤ ዳቪንቺ ኮድ በተባለው ከፍተኛ ሽያጭ ያስመዘገበ ልቦለድ መፅሐፉ የሚታወቅ ሲሆን ይሄ ልቦለድ  በዚሁ ጋዜጣ ላይ በተከታታይ እየተተረጎመ ሲወጣ እንደነበር ይታወሳል፡፡  

Published in ጥበብ

    ዮናስ አብርሃም - የ“ትንንሽ ፀሀዮች” ደራሲና አዘጋጅ    

  “የትንንሽ ፀሐዮች” ተከታታይ የሬድዮ ድራማ በድንገት መቋረጡን በተመለከተ ባለፈው ሳምንት የአዲስ አድማስ ዕትም“ጥበብ” አምድ ላይ ቃለ-መጠይቅ እንደተደረገልኝና የጣቢያው ተወካይም ምላሽ መስጠታቸው ይታወሳል፡፡
በቅድሚያ ሀሳባችንን ለማስተናገድ ዕድል ስለተሰጠን አዲስ አድማሶችን ላመሰግን እወዳለሁ። በማያያዝም፣ ከጣቢያው የተሰነዘረው ምላሽ ከዕውነታው የራቀ በመሆኑ መልስ ለመስጠት ተገድጃለሁ፡፡
ድራማውን ማቋረጥ ያስፈለገው በሁለት ምክንያቶች መሆኑ ተጠቅሷል፡፡ አንዱ ምክንያት፡- “እንደማንኛውም ድራማ የሆነ ጊዜ ተጀምሮ ማለቅ ስላለበት ነው” ተብሏል፡፡ ይህ ምክንያት በመልስነት መቅረቡ ትዝብት ላይ ይጥላል፡፡ ታስቦበት የተጀመረ ስራ በታሰበበት መንገድ መጠናቀቅ ነበረበት። ‘ማለቅ’ የሚለው ቃል ደስ አይልም፡፡ ለሕዝብ የቀረበ ትልቅ ስራ እንዲያልቅ ስለተፈለገ በጣቢያው ውሳኔ ብቻ ‘ማለቅ’ የለበትም፡፡ እንዲቋረጥ ከተፈለገ ብዙ ቀና መንገዶች አሉ፡፡ ጊዜውንና ፈቃዱን ለሰጠ አድማጭ ስሜት ማሰብ ግድ ነው፡፡ ተቀባይነት ካገኘ በኋላ ሕዝቡ ባለቤት መሆኑ አይካድም፡፡ እኔ በማይመቹ ሁኔታዎች ውስጥ ስሰራ የቆየሁት፣ አድማጩንና የሙያ ስነምግባርን አክብሬ እንጂ የሚያጓጓ ጥቅም ስላገኘሁ፣ ወይም ሌላ ዕድል አጥቼ አልነበረም፡፡
የከፈልኩትን መስዋዕትነት፣ ያደረግሁትን ልዩ ጥረት… በቅርብ ያሉ ሁሉ ይረዱታል፡፡ ሠፊው አድማጭም የሚመሰክረው ሀቅ ነው፡፡ ‘ማለቅ ስላለበት’ ብቻ ‘አልቋል’ ተብሏል፡፡ ለነገሩ “ጉመደው፣ አስወግደው” የሚሉ ቃላት አዲስ አይደሉም፡፡
ሁለተኛው ምክንያት፡- “ድራማውን ከአድማጭ በሚመጣ አስተያየት እንገመግመዋለን፡፡ ከጊዜ ወደ ጊዜ ይዘት አልባ ሆነ የሚሉ አስተያየቶች ተበራከቱ” የሚል ነው፡፡ ‘ይዘት አልባ’ የሚለው ግምገማ ግልፅ አይደለም፡፡ ከጣቢያው ምስረታ ማግስት ጀምሮ በጋዜጠኝነትና በድራማ ፀሐፊነት (Playwright) የሠራ ሰው ‘ይዘት አልባ’ ስራ ይዞ አድማጭ ፊት አይቀርብም፡፡ ድራማዎች ሁሉ አንድ ዓይነት አይደሉም፡፡ አስተያየቱ አንድ ናቸው ከሚል ድምዳሜ የመጣ ይመስላል፡፡ የዚህ ዓይነቱን አፃፃፍ በራሴ ጥረት አንብቤ የጀመርኩት እንጂ ቴክኒኩና ፈጠራው ከጣቢያው አልተሰጠኝም፡፡ ድራማው በእኛ ካላንደር (ቀን መቁጠሪያ) ከእኛ ጋር የሚራመድ ታሪክ ስለሆነ እንጂ ዝግ ብሎ መሄዱ በስንፍና የመጣ አይደለም፡፡
በገፀ-ባህርያት ላይ የተመሠረተ ወቅታዊ ድራማ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ‘ይዘት አልባ’ ፕሮግራም መስራትን ጣቢያው አላስተማረኝም፡፡ ሚዛናዊነት አንዱ የጋዜጠኝነት ማዕዘን ነው፡፡ ሚዛናዊነቱ ለእኔ ካልሰራ ምንም ማድረግ አልችልም፡፡ ከዚህ ይልቅ ሌላ ምክንያት ቢፈለግ ጥሩ ነበር። “በቃ! አልፈለግነውም” ማለት ከባድ አይደለም። በመላ ሀገሪቱ ድራማውን በጉጉትና በአድናቆት የሚከታተሉት አድማጮች ጊዜያቸውን የሠጡት ‘ይዘት አልባ’ ለሆነ ነገር ከሆነ፣ በዕድሜና በዕውቀት የሚበልጠንን ሠፊ አድማጭ አለማክበር ነው፡፡
በመሠረቱ፣ እኔ የአለቆችን ስሜት እያነበብኩ የምሰራ ሰው አይደለሁም፡፡ እንደ ጣቢያው ሁሉ፣ የእኔም መለኪያ ሕዝብ ነው፡፡ ፈራጁ ተደራሲው ስለሆነም ስሜቱን በትኩረት እከታተላለሁ፤ ባለኝ መረጃ መሠረትም በጥሩ አቋም ላይ ነበርኩ፡፡ እነማን ምን እንዳሉ እኔ አላውቅም፡፡ በእኔ በኩል ግን… ሕዝብ ያልወደደውን ነገር በግድ ለመጋት ምን ምክንያት ይኖረኛል? ብዙ የጥቅም ዕድሎችን ሰውቼ ባልተመቸ ሁኔታ ውስጥ የቆየሁት፣ ደመወዝ ከፋዩ ሕዝብ ስለሆነ ውዴታውን አክብሬ፣ ለፍላጎቱ ተገዝቼ ነው፡፡
‘ይዘት የለውም’ ከሚባል ‘ዘይት የለውም’ ቢባል በአክብሮት እቀበል ነበር፡፡ ያለ እረፍት ለአምስት ዓመታት በየቀኑ እየፃፉ፣ በየሣምንቱ እየቀረፁ መዝለቅ ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ማሰብ አለመፈለግ ለደራሲው ያለውን ስሜት ያሳያል፡፡ ሕዝብ ግን ያውቀዋል፤ አድናቆትን ብቻ አይደለም ምርቃትም ስቀበል ኖሬአለሁ፡፡
“ተዋንያኑ እየለቀቁ በመሄዳቸው ድራማው ተዳከመ” የሚል አስገራሚ አስተያየት ተሰንዝሯል። ብቸኛው ደራሲና አዘጋጅ ችግር ገጥሞኛል ብሎ ካላመለከተ፣ ችግሩ ከቁጥጥር ውጪ አይደለም ማለት ነው፡፡
ተመስገን መላኩ (ቅቤው) ወደ አሜሪካ እንደሚሄድ የተነገረው ከሦስት ዓመት በፊት ነበር። በተለያየ ምክንያት ዘግይቶ ከስድስት ወራት በፊት ለስራ ሄደ፡፡ ስለዚህ ድራማው እንዳይጎዳ በቂ ጊዜ ነበረኝ ማለት ነው፡፡ እኔ ደራሲ ነኝ፣ ደራሲ ችግሮቹን ለመፍታት ብዙ መንገድ እንዳለው የሚፅፍ ሰው ያውቀዋል፡፡ የሚወደዱ ገፀ-ባህርያት ከስራው ገለል ሲሉ መናፈቃቸው ያለ ቢሆንም ገፀ-ባህርያቱ ግን ከደራሲው ሀሳብ ስር ናቸው፡፡ ከተፈለገ፣ ግድ የሚል ችግር ቢመጣም - ባይመጣም ከድራማው የሚወጡበት አሳማኝነት ያለው ጥበባዊ መብት በደራሲ እጅ እንዳለ ይታወቃል፡፡
በረከት በላይነህ (አመዶ)፣ ‘ድራማው አይመጥነኝም ብሎ መውጣቱን’ የሰማሁት ጣቢያውን ወክለው ከተናገሩት ኃላፊ ነው፡፡ እሱ፤ አላለም - አይልም፤ ለዚህ ደግሞ መላው የድራማው አባላት ምክንያቱን ያውቃሉ፡፡ ድራማው በጥድፊያ ‘አለቀ’ ተብሎ በተነገረ በሣምንቱ በረከት (አመዶ) የሰጠውን አስተያየት ማድመጥ ይቻላል፡፡
ለጥቂት ሣምንታት ድም    ፁ ባይኖርም፣ እኔ ሊፈጠሩ የሚችሉ ችግሮችን አስቀድሜ በማሰብ ጥንቃቄ ስለማደርግ፣ ሲጀመር ከነበረው ታሪክ ጋር ተያይዞ እንዲሄድ ተደርጓል፡፡ “አመዶ የት ሀገር ነው የሄደው… ለምንድነው የሄደው?” ብዬ በመጠየቅ ‘ይዘት አልባ’ ሆነ የሚሉትን ትዝብት ውስጥ ለመክተት አልፈልግም፡፡
ዋናዋ እና ተወዳጇ ገፀ-ባህሪ ሠብለ ተፈራ (እማማ ጨቤ) ለስራ ጉዳይ እንግሊዝ ስትሄድ፣ ድራማው ጣዕሙን እንደጠበቀ አቆይቼዋለሁ፡፡ ይህንን አድማጮች ይመሰክራሉ፡፡ የእማማ ጨቤን ክፍተት ለመሙላት በጥንቃቄ ተቀርፀው የገቡት እህታቸው (እትየ ጩጩባ) በጥቂት ሣምንቶች ውስጥ ተወዳጅ መሆን የቻሉት ስላላሰብኩበት አይደለም፡፡  
እውነቱን ለመናገር ጣቢያው በእኔ ስራዎች ላይ እምነት አጥቶ፣ ጥርጣሬ አድሮበት አያውቅም። እኔ የሚጠላ ባህርይ አለኝ ብዬ ባላስብም አልተወደድኩም ብዬም አላዝንም፡፡ እንዴት መወደድ እንደሚቻል ግን አውቃለሁ፡፡
“ድራማው ካለቀ ዓመት አልፎታል” ተብሏል። ለእኔ ሲባል ከሆነ የቆየው ስህተት ነው፡፡ አንድ ግለሠብ ከመላው አድማጭና ሕዝብ አይበልጥም። ዓመት ሙሉ በሕዝብ ጆሮ ላይ ‘ይዘት አልባ’ የሆነ ድራማ ማስተላለፍ የማይመስል ነገር ነው።    ሌላው፡- “ዓመቱን ሙሉ ደብዳቤ እየፃፍን ቆይተናል” ለተባለው ደብዳቤውን ማን እንደተቀበለልኝ አላውቅም፡፡ ሁለት መልስ መስጠት ያልፈለግሁባቸው ደብዳቤዎች በግዳጅ እንደተሰጡኝ አልካድኩም፡፡
“… በነገራችን ላይ ተከታታይነት ያለው ታሪክ የያዘ ድራማ አይደለም፡፡ በየሣምንቱ አዳዲስና የተለያዩ ታሪኮችን ይዞ የሚመጣ ድራማ ነው። ስለሆነም እርሱ ቅን ቢሆንና ቢያስብበት በሦስት ሣምንት ለማጠቃለል የሚያስቸግር ነው ብዬ አላስብም” ብለዋል - የጣቢያው ተወካይ፡፡ ለዚህ ምን መልስ መስጠት ይቻላል? ብዙ ዓይነት ድራማዎች አሉ፡፡ የእኔ ድራማ ምን ዓይነት ባህሪ እንዳለው አድማጭ በሚገባ ይረዳል፡፡ “አዳዲስ ሃሳቦችን ይዞ የሚመጣ ድራማ ነው” ከተባለ በኋላ ‘ይዘት አልባ’ ነው መባሉን አትዘንጉብኝ፡፡
በሀገራችን አዲስ ባህሪ ያለው ረጅምና ተከታታይ ድራማ መሆኑን ማድነቅ ባይቻል በአግባቡ ማወቅ ግን ተገቢ ነበር፡፡ “ቅን ቢሆንና ቢያስብበት…” ለተባለው ለማቋረጥ ምን ቅንነት ያስፈልጋል፡፡ ማሰብ የነበረብኝስ ምንድን ነው?
በበኩሌ ሀሳቤን ለመሰንዘር የተነሳሁት ባሰብኩት መንገድ አልጨረስኩትም ለማለት ብቻ ነው፡፡ ቅንነትን ልጠየቅ የምገባው እኔ አልነበርኩም። ለእያንዳንዱ ነገር መልስ መስጠት ቢቻልም ቃለ ምልልሶቹን ያነበቡ ሰዎች ራሳቸው ስለሚፈርዱ ማብራሪያ ከመስጠት ተቆጥቤያለሁ፡፡
በጣም ያስገረመኝ ነገር ግን አለ፤ ለእኔ መልስ ለመስጠት የተወከሉት የፕሮግራም ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር መሆኑን አስምሩልኝ፡፡ አንድ ድምፅ ይዘው የመጡ የጣቢያው አፍ መሆናቸውን “እኛ” እያሉ በሰጡት ምላሽ ተገንዝቤያለሁ፡፡ ይሁን እንጂ በወቅቱ ስለ ስራው የሚያውቀው ማን ነበር? በስተኋላ የመጡት የአስተያየት ሰጪው የስራ ድርሻ ከዚህ ጉዳይ ጋር ባይገናኝም፣ “እኛ… የድራማው ደራሲ እሱ መሆኑን አናውቅም ነበር። … ያኛው ሰው ደራሲ ነኝ ብሎ መጥቶ ገንዘብ ይወስዳል… ይህንን ሁሉ ያወቅነው ከጋዜጠኝነት ስራው ከፋና ከለቀቀ በኋላ ነው፡፡” የሚያሳፍር ስህተት ብቻ አይደለም፡፡ ስምን አጉድፎ ስብዕናን ዝቅ ለማድረግና ለመወንጀል የታለመ ንግግር ነው። የባለቤትነትን መብት ለማጣረስ የተፈበረከ ውዥንብርና ውንጀላ ነው፡፡
የዚህ መልስ አጭርና ግልፅ ነው፡፡ “ያ-ሰው” የሚባል ፀሐፊና ገንዘብ ወሳጅ አልነበረም። የለፋሁበትን ፈርሜ የምወስደው እኔው ራሴ ነበርኩ፡፡ ይህንን ድራማ ለማስጀመር ከብቸኛ ስፖንሰር አድራጊው ዲኬቲ ኢትዮጵያ ጋር ድራማውን በተመለከተ ብዙ ስብሰባዎች የተካሄዱበትን ድርድር ከሽያጭ ክፍል ሠራተኞች ጋር በመሆን የተወጣሁት እኔ ነኝ፡፡ ሲኖፕሲስ (አፅመ-ታሪክ) አቅርቤ፣ የድራማውን ባህሪ አስረድቼ፣ ድራማው ተደማጭና ተጠቃሚ እንደሚሆኑ አብራርቼ … አየር ላይ ውሏል፡፡ ድራማው ካለቀና አለመግባባት ከተፈጠረ በኋላ በዚህ ዓይነት ስም ማጥፋት በአደባባይ መቅረብ ተገቢ አይደለም፡፡  
ድራማው እንዴት እንደተጀመረ፣ በምን መንገድ እንደተጀመረ፣ ሲጀመር ለትንሽ ጊዜ በብዕር ስም ለምን እንደፃፍኩ… እዛው ቢጠይቁ ኖሮ መልስ ያገኙ ነበር፡፡ በብዕር ስም ፅፌ ክፍያዬን ስቀበል ይኼ የመጀመሪያዬ ነው እንዴ? እኔስ የመጀመሪያው ሰው ነኝ?! አይደለሁም፡፡
ምንም እንኳን ለውስጥ ሰራተኞች ተጨማሪ ክፍያ የማይታሰብ ቢሆንም በጋዜጠኝነት እየሰራሁ ለድራማው ‘በደቂቃ 20 ብር’ ይከፈለኝ የነበረው ልዩ ተሰጥዖን የሚጠይቅ ስራ ስለሆነ ነው፡፡ የመስሪያ ቤቱ  ባልደረባ የመዝናኛ ክፍል ኃላፊ ሆኜ ድራማውን መፃፍና ማዘጋጀት ስጀምር፣ ከደመወዜ በተጨማሪ 1,800 ብር የሚከፈለኝ በጋዜጠኝነት እንጂ በደራሲነት ስላልተቀጠርኩ ነው፡፡ ከ70ኛው ክፍል በኋላ ድርጅቱን ለቅቄ ስወጣ፣ በደቂቃ 80 ብር እንዲከፈለኝ ተስማምተናል፡፡ የመጨረሻዎቹን አስራ ስድስት ወራት አካባቢ ደግሞ ክፍያዬ በደቂቃ 100 ብር ደርሷል፡፡ በጠቅላላ በወር 10 ሺህ ብር ማለት ነው፡፡
ለተሰጥኦ (Talent) ብዙ እንደሚከፈል መንገር አይገባኝም፡፡ ተወካዩ ከፍተኛ ገንዘብ ያሉት ይህንን ከሆነ፣ ውጪ ያለውን ገበያና ክፍያ አያውቁትም ማለት ነው፡፡  
ሠብለ ተፈራ በእማማ ጨቤ ገፀ-ባህሪ ተዋናይነቷ፣ በኋላ ላይ ጭማሪ ተደርጎላት እንኳ በወር የምትወስደው 2 ሺህ ብር አይሞላም፡፡ ሁላችንም ስለ ገንዘብ ሳይሆን ስለ ሙያው ፍቅር እንደምንሰራ ጣቢያው አልተረዳም፡፡
“ድራማው የኛ ነው” ማለት በጣም ያስገምታል፡፡ ጣቢያው በድራማው ላይ ያለውን ባለቤትነት ማወቅ ካስፈለገ… ወጪ ስላወጣበት እና ገንዘብ ከፍሎ ስላሰራ ብቻ ነው፡፡ ይሄ ማለት ደግሞ እስካሁን በተቀረፁት ላይ ሙሉ ባለቤትነት እንዳለው ግልፅ ነው፡፡ መረዳት የሚያስፈልገው ነገር የአንድ ደራሲ የአዕምሮ ፈጠራ ውጤት እንደመሆኑ፣ ቢያስፈልግ ፅሁፉን በሌላ ስቱድዮ በራስ ወጪ በመቅረፅ መጠቀም ይቻላል፡፡
በቀጥታ ያልተዋዋልንበት የስራ ግንኙነት ተቋርጧል፡፡ ለአመታት የተላለፉትን መደምሰስ ከተፈለገ ችግር የለም፡፡ ገፀ-ባህሪያቱን ግን ማክሰም አይቻልም፡፡ የአዕምሮዬ ውጤት የሆኑት ገፀ-ባህሪያት ባለቤት እኔው ብቻ ነኝ፡፡
ጣቢያው ትልቅ ቢሆንም ከዕውነትና ከሕግ በላይ ሊሆን አይችልም፡፡ አሁንም እላለሁ፡- “በእኔ በኩል ድራማውን ፅፌ አልጨረስኩም!!”          

Published in ጥበብ

በአሜሪካ ፊላዴልፊያ ውስጥ በሚገኘው የቴምፕል ዩኒቨርሲቲ የህክምና ትምህርት ቤት በማስተማር ላይ የሚገኙት ኢትዮጵያዊው ዶክተር ኤልያስ ሲራጅ፣ በሙያቸው ላበረከቱት ጉልህ አስተዋጽኦ ከአሜሪካ ክሊኒካል ኢንዶክሪኖሎጂስትስ ማህበር የላቀ አገልግሎት ሽልማት አገኙ፡፡
በኢንዶክሪን ህክምናና በአጠቃላይ ጤና መስፋፋት ዘርፍ የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱና በአሜሪካም ሆነ በሌሎች አገራት የሚገኙ በቂ የጤና ግልጋሎት ያላገኙ ህዝቦችን በአመራር ሰጪነት፣ በማያሰልስ ቁርጠኝነት፣ በራዕይ፣ በፈጠራና ተጽዕኖ በሚፈጥር መልኩ በማገልገል፣ ብቃታቸውን ላሳዩ የተመረጡ ባለሙያዎች የሚሰጠው ይህ ሽልማት፣ ባለፈው ሳምንት ላስ ቬጋስ ውስጥ ለዶክተር ኤልያስ ተበርክቷል፡፡
“በቂ የህክምና ግልጋሎት ያላገኙ በርካታ ዜጎች ካሉባት አገር እንደመውጣቴ፣ በቻልኩት መንገድ ሁሉ ህብረተሰቡን የማገልገል ሃላፊነት እንዳለብኝ ይሰማኛል። ማህበሩ በአገሬ በኢትዮጵያና በአሜሪካ የሚኖሩ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ላከናወንኳቸው ተግባራት እውቅና ሰጥቶ ሽልማቱን ስላበረከተልኝ ክብርና ኩራት ይሰማኛል።” ብለዋል ዶ/ር ኤልያስ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ፡፡ ዶ/ር ኤልያስ የህክምና ተማሪዎችን፣ ማህበረሰቡንና በኢትዮጵያ በሚገኙ አምስት የህክምና ትምህርት ቤቶች ውስጥ የነበሩ ተለማማጆችን ተጠቃሚ ያደረጉ ስራዎችን ማከናወናቸውና በአገሪቱ የመጀመሪያውን የኢንዶክሪኖሎጂ ስልጠና ፕሮግራም በማስጀመር ረገድ ቁልፍ ሚና መጫወታቸው ይነገራል፡፡  
በአሁኑ ሰዓት በቴምፕል ዩኒቨርሲቲ የህክምና ትምህርት ቤት በመምህርነትና በዩኒቨርሲቲው የኢንዶክሪኖሎጂ ፌሎውሺፕና የዲያቤቲስ ፕሮግራሞች ዳይሬክተርነት በማገልገል ላይ የሚገኙት ዶ/ር  ኤልያስ፤ ለታካሚዎች ነጻ እንክብካቤ በመስጠት፣ በኢትዮጵያ ያለውን የስኳር በሽታ በተመለከተ ጉልህ ምርምር በማካሄድና በኢትዮጵያና በአሜሪካ የህክምና ተቋማትና ባለሙያዎች መካከል ያለውን ትብብር ለማጠናከር የሚሰሩ ድርጅቶችን በመምራት ይታወቃሉ፡፡
በጎንደር የህክምና ሳይንስ ኮሌጅ ትምህርታቸውን ተከታትለው ከጨረሱ በኋላ፣ ነጻ የምርምርና የስልጠና ዕድል አግኝተው ወደ ጀርመን በማምራት ሊፕዚንግ ዩኒቨርሲቲን የተቀላቀሉት ዶ/ሩ፤ በመቀጠልም ወደ አሜሪካ በማቅናት በክሌቭላንድ ክሊኒክ በተግባር የታገዘ ስልጠና ወስደዋል፡፡
በኢንዶክሪኖሎጂና የውስጥ ደዌ ህክምና የብቃት ማረጋገጫ ያላቸው እኒህ ዶ/ር፣ በተለያዩ የሙያ ማህበራት ውስጥ በአባልነትና በቦርድ አባልነት ንቁ ተሳትፎ በማድረግና በተለያዩ አለማቀፍ መድረኮች ላይ እየተጋበዙ ሙያዊ ንግግሮችን በማቅረብ ይታወቃሉ። በርካታ የህክምና ምርምር ጽሁፎችን ለህትመት ያበቁ ሲሆን በቴምፕል ዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው በመምህርነት ባበረከቱት አስተዋጽኦ የላቀ የመምህርነት ሽልማት ከዩኒቨርሲቲው ተቀብለዋል፡፡

ቫይታሚኖች ሰውነታችንን ዕድገት ተፋጠነ ለማደስረግ፣ ከበሽታ ለመከላከል፣ ከውጥረት እና ተያያዥ ችግሮች ሰውታችንን ለመጠበቅ የህዋሳቶቻችንን የመከፋፈልና መራባት ሂደት በማገድ ዘርን ተክቶ ለማለፍና ልጅ ለመውለድ የሚያስፈልጉ ቅድመ ሁኔታዎችን በማመቻቸት ረገድ ከፍተኛ ጠቀሜታዎች አሏቸው፡፡
ለሰውነታችንና አስፈላጊ የሆኑ ቫይታሚኖች በአብዛኛው በሰውነታችን ውስጥ የሚሰሩ ሲሂን ከምንመገባቸው ምግቦችና መጠጦች የምናገኛቸው የቫይታሚን አይነቶችም አሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በፋብሪካ ተመርተው በእንክብል መልክ አልያም በፈሳሽ ሸሮች መልክ እየተሰሩ በጥቅም ላይ የሚውሉ የቫይታሚን አይነቶችም አሉ፡፡ ለሰውነታችን ከሚሰጡ ጠቀሙታ አንፃር በስፋት በቀጥታም ላይ ከሚውሉት ቫይታሚን አይነቶችና አገልግሎቶቻቸው ጥቂት ልንሳ ወደድን፡፡
ቫይታሚን ኤ
እይታዎ የተሟላና የተስተካከለ እንዲሆን ይረዳዎታል፡፡ የቆዳዎ ጤና እንዲጠበቅ በማድረጉ ረገድም ጠቀሜታው ከፍ ያለ ነው፡፡ ህዋሳቶቻችን በመደበኛ ሁኔታ ማደግና መራባታቸውን ይቆጣራል፡፡ ጀልጅ መውለድ ጋር የተያያዙ ሂደቶችን የተሟሉና ውጤታማ የሆኑ በማድረጊ በኩልም ትልቅ አስተዋፅኦ አለው፡፡
 የቫይታሚን ኤ መገኛዎች
ወተት ጉበት ብርቱካን አበባ ጎመን ካሮት የተለያዩ አትክልቶች በምላስ ዝርዝረዎ ውስጥ መኖራቸውን ልብ ይበሉ፡፡
ቫይታሚን ቢ
ድካም፣ አቅም ማጣት፣ በቀላሉ መዛል የቫይታሚን ቢ የተለያዩ መልኮችና አይነቶች አሉት፡- ቫይታሚን ቢ፣ በ2፣ቢ6፣ቢቢኒያሲን እና ፎሊክ አለደ ዋንኞቹ የቫይታሚን ቢ አይነቶች ናቸው። ቫይታሚን ቢ ቀይ የደም ህዋሳትን በማዘጋጀትና ኦክስጅንን በሰውነት ውስጥ በማዘዋወር ሂደትም ቫይታሚን ቦ ወሣኝ ሚና አለው፡፡ የቫይታሚን ቢ ወሣኝ ሚና አለው፡፡ የቫይታሚን ቢ እጥረት እጅግ አደገኛ ለሆነ የጤና ችግር የሚዳርግ በመሆኑም ሃኪሞች ብዙ ጊዜ ቫይታሚን ቢ ኮምክሎክሰን ለህመምተኞቻቸው ያዛሉ፡፡
ቫይታሚን ቢ የት ያገኛል
አሣ፣ ስንዴ፣ አጃ፣ እንቁላል፣ ወተትና የወተት ተዋፅኦዎች፣ አተር፣ ባቄላ ሥጋ፣ የቫይታሚን ቢ ዋንኛ ምንጮች ናቸው፡፡
ቫይታሚን ሲ
የሚደማ ድድ፣ የሚላጥና የሚቆስል ቆዳ አልዎት? እንግድያውስ የቫይታሚን ሲ እጥረት አለብዎት ማለት ነው፡፡ ቫይታሚን ሲ የቆዳዎቻችንና ድዳችንን ጤና በመጠበቁ ረገድ ከፍተኛ ሚና አላቸው፣ ኢንፌክሽን በሰውነታችን ላይ የከፋ ጉዳት እንዳያስከትልም ቫይታሚን ሲ ከፍተና እገዛ ያደርጋል፡፡
የቫይታሚን ሲ መገኛዎች
ሎሚና ብርቱካን፣ ስትሮበሪ፣ ቲማቲም፣ ጎመን፣ ሚጥሚጣና በርበሬ በቫይታሚን ሲ የበለፀጉ የምግብ አይነቶች ናቸው፡፡
ቫይታሚን ዲ
ቫይታሚን ዲ በሰውነታችን ውስጥ የሚዘጋጀው ከፀሐይ ብርሃን አልትራናዮሴት ጨረሮችን በቆዳ አማካኝነት በሚያገኝበት ወቅት ነው፡፡ ቫይታሚን ዲ የአጥንትን ጥንካሬ ይጠብቃል፡፡ የዚህ ቫይታሚን እጥረት የአጥንት መሳሳትን ያስከትላል፡፡
ቫይታሚን ዲ ከፀሐይ ብርሃን በተጨማሪ ከወተትና ከወተት ተዋፅኦዎች እንዲሁም ከተለያዩ ጥራጥሬወፐች ማግኘት ይቻላል፡፡  

Published in ዋናው ጤና

በትምህርት፣ በሆቴልና  በአስጎቢኝነት ዘርፎች ተሰማርቷል
በአፍሪካ ስመጥር ዩኒቨርሲቲ ለመገንባት አቅዷል

የመጀመሪያ ዲግሪውን ያገኘው በአካውንቲንግ ነው፡፡ በአገሩ ሕንድ በዚሁ ሙያ አስተማሪ ነበር። ሁለተኛ ዲግሪውን ካገኘ በኋላ ከማስተማር በተጨማሪ የማማከር አገልግሎትም ይሰጥ እንደነበር ገልጿል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ የመጣው በ2001 (እ.ኤ.አ) ሲሆን የያኔው ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በመምህርነት ቀጥሮት ነበር፡፡ ሆኖም በኮሌጁ ከሦስት ዓመት በላይ አልቆየም፤ ጥሎ ወጥቶ የራሱን ቢዝነስ ጀመረ፡፡
ታሪኩን የማወጋችሁ ህንዳዊ፤ የስሪ ሳይ (SRI SAI) ኮሌጅ፣ ደንበል ሲቲ ሴንተር ፊት ለፊት አበሩስ ህንፃና ኦሎምፒያ አካባቢ የሚገኙት ስሪ ሳይ የእንግዳ ማረፊያና ሆቴል እንዲሁም በተመሳሳይ ስም የሚጠራው የአስጎብኚ ድርጅት ባለቤት ሚ/ር ረዲ ኤል ጂ ነው፡፡
የ41 ዓመት ጎልማሳ የሆነው ሚ/ር ረዲ፤ አዲስ አበባ መኖር ከጀመረ 13 ዓመት አስቆጥሯል፤ የ28 ዓመት ወጣት ሳለ ነበር ወደ ኢትዮጵያ የመጣው፡፡ አገሪቷ ከሰሩባት ለዜጎቿ ብቻ ሳይሆን ለእንግዶችም ትመቻለች ማለት ነው ያሉት የቀድሞ የዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ መምህር ስለ ሚ/ር ረዲ ሲናገሩ፣ “ሚ/ር ረዲ የሚደንቅ ሰው ነው፡፡ ከእሱ ብዙ መማር ይቻላል፡፡ ከዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ የለቀቀው ከኮሌጁ ባለቤት  ከዶ/ር ፍስሐ እሸቱ ጋር ባለመስማማቱ አባርሮት ነው፡፡ እሱ ግን ኢትዮጵያ ለቢዝነስ ምቹ መሆኗን ተገንዝቦ ስለነበር፣ አገሩ ሄዶ በራሱ መንገድ ተመልሶ መጣ፡፡ ይኼው አሁን ጥሩ እየሰራ ነው፡፡ ለራሱ ብቻ ሳይሆን ለአገርና ለዜጎችም ጥቅም ፈጥሯል፡፡ ያኔ አገሩ እንደተመለሰ በተሸናፊነት ስሜት ቀርቶ ቢሆን ኖሮ ይሄ ሁሉ የለም፡፡ ሚ/ር ረዲ መጥፎ አጋጣሚን ወደ መልካም እድል የለወጠ ሰው ነው፣ ከእሱ ብዙ መማር ስለሚቻል ላማክረው አስቤአለሁ” ብለዋል፡፡
ሚ/ር ረዲ እንዴት ወደ ቢዝነስ እንደገባ ሲያስረዳ፣ “በወቅቱ መንግሥት የውጭ ኢንቨስተሮች መጥተው በአገሪቷ እንዲሰሩ ይፈልግ ነበር፡፡ ይህም ጥሩ አጋጣሚ ሆነኝ፡፡ በፊትም የማማከር ልምዱ ስለነበረኝ፣ ከአገሬና ከመላው ዓለም ኢንቨስተሮች አምጥቼ ቢዝነስ እንዲጀምሩ ለማድረግ በእንቅስቃሴያቸው ልረዳቸው የምችልበትን የአማካሪ (ኮንሰልተንሲ) ድርጅት በ2004 (እ.ኤ.አ) በ50ሺ ዶላር ከፈትኩ” ብሏል፡፡
በማማከሩ ሥራ ሁለት ዓመት ከሠራ በኋላ ሌላ አጋጣሚ ተፈጠረ፡፡ ቀደም ሲል ሲያስተምራቸው የነበሩ ጎበዝ ተማሪዎች “የማስተርስ ፕሮግራም መቀጠል እንፈልጋለን፣ ለምን አትጀምርም?” ሲሉ ጠየቁት፡፡ የማስተርስ ፕሮግራም መማር የሚፈልጉ ተማሪዎች ቁጥር ብዙ ስለነበር “ገበያው ጥሩ ከሆነ ለምን አልጀምርም?” የሚል ሐሳብ መጣለት። ማሰብ ብቻ ሳይሆን “መክፈት ካለብኝ፣ በአገሬ በትምህርት አሰጣጥ ጥራት በጣም ጥሩ ስም ካለው ዩኒቨርሲቲ ጋር ነው መሥራት ያለብኝ” በማለት ወሰነ። ከዚያም በሕንድ ታዋቂ የሆነውን ስኪም ማኑፖል ዩኒቨርሲቲን አነጋገረ፡፡ ከፍተኛ የትምህርት ተቋሙም በአዲስ አበባ በስሙ ዩኒቨርሲቲ እንዲቋቋም ስለተስማማ፣ በ2006 (እ.ኤ.አ) ሴሪ ሳይ ኮሌጅን በመክፈት የማስተርስ ፕሮግራም መጀመሩን ሚ/ር ረዲ ይናገራል፡፡
ኮሌጁ ትርፋማ እየሆነ ሲመጣ፣ ለምን በሌላስ ዘርፍ አልሞክርም? በማለት የእንግዳ ማረፊያና ሆቴል በ2008 ዓ.ም ከፈተ፡፡ ከዚያም ኮሌጁን በማስፋፋት ከማስተርስ ፕሮግራም በተጨማሪ በመጀመሪያ ዲግሪ የሚያስተምር ኮሌጅ አቋቋመ። ቢዝነሱ እየሰመረለት ሲሄድ የበለጠ ማስፋፋት ፈለገ። ስለዚህ ከእንግዳ ማረፊያና ከሆቴሉ ጋር የሚሄድ ነገር አሰበና፣በቀጣዩ ዓመት አስጎብኚ ድርጅት ከፈተ፡፡ አሁን ሚ/ር ረዲ በትምህርት፣ በሆቴል፣ በእንግዳ አቀባበልና መስተንግዶ ዘርፎች ተሰማርቶ እየተጋ ይገኛል፡፡
ኮሌጁ በመጀመሪያ ዲግሪ አካውንቲንግ፣ ቢዝነስ አድሚንስትሬሽንና ኮምፒዩተር ሳይንስ እያስተማረ ነው፡፡ የትምህርት መርሐ ግብሩ ያነሰው የተለያየ ትምህርት የሚሰጡ ተፎካካሪ ኮሌጆች በየጊዜው ስለሚከፈቱ እንደሆነ ሚ/ር ረዲ ይናገራል፡፡
ስሪ ሳይ ሲኪም ማኑፖል ዩኒቨርሲቲም ለማስተርስ ፕሮግራም መደበኛና የተልዕኮ ትምህርቶችን ይሰጣል፡፡ በመደበኛው ማስተርስ ኦፍ ኮምፒዩተር ሳይንስ፣ ማስተርስ ኦፍ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ ማስተርስ ኦፍ ቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን ያስተምራል፡፡ በተልዕኮ ደግሞ ማስተርስ ኦፍ ቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን (ኤምቢኤ)፣ማስተርስ ኦፍ ኮምፒዩተር ሳይንስ፣ ማስተርስ ኦፍ ኢንፎርሜሽን ሳይንስ፣ ማስተርስ ኦፍ ጆርናሊዝም ኤንድ ማስ ኮሙኒኬሽን ይሰጣል፡፡ ለማስተርስ ዲግሪ የምናስከፍለው ዋጋ ተመጣጣኝ ነው ያለው ሚ/ር ረዲ፤ ለመደበኛ ማስተርስ ዲግሪ 38ሺ ብር፣ ለተልዕኮው ደግሞ 48 ሺህ ብር መሆኑን ገልጿል። ኮሌጁ ቀደም ሲል ለበርካታ ተማሪዎች ነፃ የትምህርት ዕድልና የኪስ ገንዘብ (ፖኬት መኒ) መስጠቱን የጠቀሰው ባለሀብቱ፤ አሁንም ሁለት መስፈርቶችን የሚያሟሉ ተማሪዎችን ተቀብሎ በነፃ ለማስተማር ዝግጁ መሆኑን ገልጿል፡፡ አንደኛው መስፈርት ከፍተኛ ውጤት ኖሯቸው በድህነት ወይም በሌላ ችግር ምክንያት ከፍለው መማር ለማይችሉ ወጣቶች ነው፡፡ ሌላው በሚሰለጥኑበት የትምህርት ሙያ ማኅበረሰባቸውን ማገልገል ለሚፈልጉ የገጠር አካባቢ ወጣቶች ነው፡፡ ሚ/ር ረዲ መመዘኛውን የሚያሟሉ ገርጂ በሚገኘው የኮሌጁ ጽ/ቤት እንዲመዘገቡ ጠቁሟል፡፡
የአስጎብኚነት ስራው አትራፊ ባይሆንም አክሳሪ ግን አይደለም፡፡ የቱሪዝም ሥራ ከመሰረተ ልማት መሟላት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ መንገድ፣ ንፁህ የመጠጥ ውሃ፣ መብራት፣ የቴሌኮሙኒኬሽን መገናኛ፣ ንፁህ ማረፊያ ሆቴል፣ ጥራቱን የጠበቀ ምግብ፣ … ይፈልጋል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ እነዚህ ነገሮች የተሟሉ አይደሉም፡፡ በዚህ ላይ በአሁኑ ወቅት የዓለም ኢኮኖሚ ሙሉ በሙሉ ከድቀት ስላልወጣ፤ የቱሪስቶችን ቁጥር ለማሳደግ  እያላመድን ነው ብሏል፤ ሚ/ር ረዲ፡፡
ኢንቨስተሩ ወደፊት በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በመላው አፍሪካ ስመ ጥርና ገናና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የመገንባት እቅድ አለው፡፡ ለዚህ ዩኒቨርሲቲ መገንቢያ የሚሆን ቦታ ከመንግስት ጠይቋል፡፡ “መንግስት የጠየቅሁትን ቦታ ከሰጠኝ እሰየው ነው፡፡ ባይሰጠኝ እንኳ መሬት ከግለሰብ ገዝቼ እሰራለሁ እንጂ እቅዴ አይቀርም” በማለት ቁርጠኝነቱን ተናግሯል፡፡
ኢትዮጵያ በፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ብትሆንም ከተቀሩት የአፍሪካ አገራት የዕድገት ማነቆዎች የፀዳች አይደለችም ይላል ሚ/ር ረዲ። ብዙ ችግሮች ቢኖሩም የካፒታል አቅርቦትና የባለሙያ እጥረት፣ የምርታማነት ማነስ፣ ወጥ ፖሊሲ ያለመኖር፣… በዋናነት እንደሚጠቀሱ ገልጿል፡፡ እነዚህን ችግሮች ለማለፍ የሚቻለው ሁሉም ሰው ለዚህች አገር ቀና አስተሳሰብ ሲኖረው ነው ብሏል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፤ ሁሉም ሰው በተገኘው ለውጥ ረክቶ ከመቀመጥ ይልቅ ለተሻለና ለበለጠ ለውጥና ዕድገት በርትቶ  መስራት አለበት ሲልም ምክሩን ለግሷል፡፡
ሚ/ር ረዲ በአሁኑ ወቅት ከ120 እስከ 150 ላሉ ዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ ገቢውም እያደገ መሆኑን ተናግሯል፡፡            

Saturday, 24 May 2014 14:39

የጉዞ ማስታወሻ

ገፅ ለገፅ! [Interface Meeting]
ተፋጠጥ፣ ተገላለጥ፣ ተሞራረድ፣ ችግር ፍታ!


የዛሬው የጉዞ ማስታወሻዬን ለየት የሚያደርገው ኃላፊነት በመውሰድና በተጠያቂነት ላይ ባተኮሩ ሁለት ስብሰባዎች ላይ መሳተፌ ነው - አንዱ ብሾፍቱ/ ደብረዘይት ነው፡፡ ሁለተኛው ድሬዳዋ ነው፡፡
ሁኔታው እጅግ እንዲያስደምመኝ ያደረገው፤
1ኛ/ ህዝብ አንዳችም ወደኋላ ሳይል ብሶቱን፣ ምሬቱንና ጥያቄውን ለማቅረብ መቻሉ፤
2ኛ/ መንግሥት በቀጥታ ይሄ የሆነው በዚህ ምክንያት ነው፡፡ ለዚህ ይቅርታ አድርጉልን፤ አልሠራነውም፡፡ ይሄንን በትክክል ሠርተናል፡፡  ይሄ መንገድ ላይ ነው ትንሽ ታገሱን ለማለት መቻሉ ነው።
በባለሙያዎቹ ቋንቋ ህዝብ “አገለግሎት ተቀባይ”፣ መንግሥት “አገልግሎት ሰጪ” ነው የሚባለው፡፡ ሁለቱ ፊት ለፊት የተገናኙበትን ሁኔታ “ገፅ ለገፅ” የሚሰኝ ርዕስ ሰጥተውታል - ፕሮጄክታውያኑ፡፡
ነገሩ የተካሄደው ብሾፍቱ/ደብረዘይት ውስጥ ነው፡፡ በተገልጋይ ወገን ህዝቡ፡፡ በአገልጋይ ወገን ቁንጮው ከንቲባ ሆነው፤ የየዘርፍ ኃላፊዎችና የወረዳና ቀበሌ ሹማምንት ተገኝተዋል፡፡ እንደዚህ ስብሰባ የማረከኝ ወደግልጽነት የሚያመራ ጉባዔ አላጋጠመኝም፡፡ ተግባር ሌላ ጉዳይ ነው ብዬ ማለት ነው፡፡
የብሾፍቱን (የደብረዘይቱን) ገፅ ለገፅ (interface) ፕሮግራም ሳይ ትዝ ያለኝ፤ አንድ ጊዜ አቶ ሃይማኖት ዓለሙ በቴሌቪዥን ማቅረብ ጀምሮ የነበረው ፕሮግራም ነው፡፡ ነገር ነገሩ አልቀጠለም እንጂ እንደ የአበሻ “ሀርድ-ቶክ” መሆኑ ነበር፡፡ አሁን ያየሁት የደብረዘይት “ገፅ-ለገፅ” ከዚያኛው የሚለየው፣ ያኛው አንድ ሰው ለአንድ ሰው የሚያደርገው ሲሆን፤ ይሄኛው ግን አገልግሎት ተቀባይ ህዝብ እና የመንግሥት ኃላፊዎች ግንባር ለግንባር የሚጋጠሙበት፣ የሚተቻቹበት፣ ነገሩን የሚያፍረጠርጡበት፤ መፍትሄ ለመስፍጠርም ከማን ምን ይጠበቃል? የሚባባሉበት፤ ህይወት ያለው ውይይት ነው፡፡ በመጨረሻ ጉዳዩን መሬት አውርዶ የሚተገብርና የሚከታተል የተግባር ኮሚቴ የሚመሰርትበት ነው፡፡
የከተማይቱ ዋና ችግር የውሃ እጦት ነው። እንደ ብሾፍቱ ላለች በውሃ ለተከበበች ከተማ ጉዳዩ የአባይን ልጅ ውሃ ጠማው ነው፡፡ ሁለተኛው መነጋገሪያ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ነው፡፡ ቡጥ ቡጡን ወደኋላ ላይ እተርክላችኋለሁ፡፡ ብዙ ትምህርት - ተኮር ችግሮች ተወስተዋል፡፡  
“ሬሣ እንኳ አጥበን አንቀብርም!”
ከአገልግሎት ተቀባዩ ህዝብ መካከል ልቤን የነኩኝ አንድ ሴት አይቻለሁ፡፡ የውሃ ችግርን ለማሳየት ከዚህ የተሻለ አገላለፅ አላጋጠመኝም፡፡ እንዲህ ነበር ያሉት፡-
“ዛሬ የምታዩትን ነጭ ሸማ ለብሼ የመጣሁት ለዚህ ስብሰባ ስል ነው፡፡ የክት ልብሴን አውጥቼ ለብሼ ነው የመጣሁት፡፡ የሰፈሩ ሰው ሁሉ ያቃል ይህን ለብሼ እንደማላውቅ፡፡ ቆሻሻ፣ አዳፋ ልብስ ነው የምለብሰው - ከወር ወር የማይታጠብ፡፡ ምነው ቢባል በምን ውሃ አጥበን እንልበስ! እናንተ ስለ ልብስ ሳወራ የውሃን ችግር በቀላሉ ታዩ ይሆናል፡፡ ዛሬ እኛ ሬሳ አጥበን አንቀብርም!
አንድ ጀሪካን ውሃ 20 ብር ነው /ሸክሙን ትተን/!!  ሁሉ ነገር ከአቅማችን በላይ ነው ይሉናል ለሚመለከታቸው ስንነግር፡፡ 98 ከመቶ ደርሰናል ይሉናል 40ውን ብቻ ለእኛ ይስጡን፡፡ (ተሰብሳቢው በሳቅና በውካታ ተሞላ!) በሽንት ቤት ሽታ አስም ከያዘኝ ቆየሁ፡፡ የቆሻሻ ማንሻ መኪና የለም! ቢኖርም የግለሰብ ነው፡፡ በአመድና ቆሻሻ ክምር፣ በሽንት ቤት ጠረን ውስጥ የምንኖረው ከሙታኖች በላይ ብቻ ነው፡፡ እኛ የ08 ነዋሪዎች ነን! ቅድም እንዳልኩት ሬሳ እንኳ አጥበን አንቀብርም!”
ልብ በሉ እኒህ ሴት ግልፅ በግልፅ የሚናገሩት ፊት ለፊታቸው ለተቀመጡት ለከተማይቱ ከንቲባ ለአቶ ከፍያለው አያና እና ለውሃ፣ ለትምህርት፣ ለጤና ሴክተር ባለስልጣናት ነው፡፡ ይሄ ነገር ምነው በሀገሪቱ ሁሉ እንዲሁ ቢቀጥል፤ አልኩኝ በሆዴ፡፡
የከተማይቱ ከንቲባ የመለሱትም የዋዛ አደለም። ችግሩ ሲገለፅ መቀበል፣ መፍትሔ እጅ - በጅ መስጠት የሚችሉ ከንቲባ ናቸው፡፡ በፊት ለፊት መፍትሔውን መጠቆምና ግልፅ ውሳኔ ለማበርከት ይችላሉ፡፡ “የስራ ተቋራጮቻችን እየዋሹ ሲያስዋሹን ነበር” ሲሉ ሰው በሳቅ ፈነዳ። “ገፅ በገፅ በመነጋገራችን መንግስትም ህዝብም ተጠቃሚ ነው፡፡ ዋናው ግን ህዝብ ነው፡፡ ህዝባችን ችግሩን ማወቅ አለበት! ስኬቱ የህዝብ ስኬት ነው!፡፡ ክፍተቱም የህዝብ ክፍተት ነው!
ሁሉም የየድርሻውን ይወስዳል!...
“… የኃላፊነትና የተጠያቂነት ስብሰባ ትልቁ ጥቅሙ እንደግለሰብ ልናገኛቸው የማንችላቸውን የመንግስት ኃላፊዎች በግልፅ ማግኘታችን ነው። ስለዚህ ሐሜት ይወገዳል፡፡ ሁሉም የየድርሻውን ይወስዳል…98% ስራ መገባደዱ እውነት ነው ግን አገልግሎት ካልሰጠ ዋጋ የለውም፡፡ የውሃውን ችግር ታሪክ እናደርጋለን! ሆኖም የአቅማችንን ብቻ ነው የምናደርገው ታገሱን!
ረዥም በማይባል ጊዜ እንጨርሰዋለን፡፡ በቂ ውሃ አዘጋጅተናል፡፡ ስለዚህ ተስፋ አለን፡፡
የፍሳሽ ቆሻሻን ችግር እንደ ቤት ሥራ ለመውሰድ ቃል እንገባለን፡፡ በትምህርት ጉዳይ ህዝቡም መገምገም አለበት፡፡ የትምህርት ጉዳይ የእያንዳንዱ ቤተሰብ ጉዳይ ነው፡፡ ለመምህሩም ተገቢው አክብሮት ሊሰጠው ይገባል፡፡ የጎረቤት ልጆች የእኔም ልጆች ናቸው ለማለት መቻል አለብን፡፡…”
“በት/ቤት ቅፅር ግቢ ያሉ የመኖሪያ ቤቶችን በተመለከተ አሁኑኑ ውሳኔ እንስጥ” አሉና፤
“እኛ/መንግሥት/ ቦታ እናዘጋጅ፡፡ ቤት መስራት ለማይችሉ ቤት እንስጣቸው፡፡ ግቢውን ለት/ቤት ብቻ እናድርገው፡፡ ይኸው በፊት ለፊት የትምህርት ቢሮ ኃላፊዎች ኃላፊነቱን ይወስዳሉ፡፡
በ3 ወር ጊዜ ውስጥ ውጤቱን እናመጣላችኋለን!...” ጭብጨባው ቀለጠ፡፡ ዕውነት ለመናገር አንድ የመንግሥት ባለሥልጣን እንዲህ ገፅ በገፅ የሚችለውን እችላለሁ፣ የማልችለውን አልችልም፤ ሲል ማየትና መስማት በበኩሌ የለውጥ ሀሁ ተጀመረ ፤ አሰኝቶኛል፡፡  
ከንቲባው ቀጥለው፤ ወደትምህርት ትኩረታቸውን አዙረው፤
“ተማሪ ለመማር 5 ሣንቲም መክፈል የለበትም። የሚያስከፍል ካለ ወንጀለኛ ነው!!” አሉ፡፡
“ከህዝቡ የሚጠበቀውስ?” አሉ ቀጥለው። “የትምህርት ሂደቱን መደገፍ! 50% የድምር ወጪውን ህዝቡ እንዲሸፍን ተነጋግረናል፣ ወስነናል፣… በጉልበት፣ በጊዜ፣ በገንዘብ! ተግባራዊ እናድርገው። ውሃ ሲፈስ ብታዩ የምትጠቁሙ እነማን ናችሁ? አለቃ ሲሰርቅ እምቢ /No!/ የምትሉ እነማናችሁ? የራሳችሁ ሀብት ነው ሚሰረቀው! እንደዛ ከሆነ ብሾፍቱ የጥቂት ሰዎች ናት ማለት ነው! ከህዝብ የማያስፈልገን ሰው የለም! አቅም ትሆኑናላችሁ ኑ! ያደግንበት አካባቢ ለፈጣን ዕድገት አመቺ አልነበረም አይፈቅድም፡፡ መለወጥ አለበት። አንዱ አንዱን አይርገም! ዛሬ ማይክሮ - ሰከንድ ሚሊዮን ያሳጣል፡፡ እንፍጠን፡፡…” ተቀባይነታቸው አያጠያይቅም፡፡
*       *        *
ይሄ ሁሉ የሚወራበት ስብሰባ፤ ርዕሱ፤ “የዜጐችና የመንግሥት ተወካዮችና ባለሥልጣናት “የውሃ፣ የአካባቢ ፅዳትና የመጀመሪያ ደረጃ አገልግሎት፤ የብሾፍቱ ወርክሾፕ ሲሆን፤ የፕሮግራም መሪው ባስረዱት መሠረት (ፕሮግራሙ ላይም አለ) በመጀመሪያ የእየሩሳሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት ሥራ አስኪያጅ አቶ ሙሉጌታ ገብሩ የመክፈቻ ንግግር ያደርጋሉ፡፡ ከዚያ በየጉዳዩ ላይ ጥናት የሚያቀርቡ ይኖራሉ፡፡ በአጥኚዎች የ06/ 07/ 08/ 09 ቀበሌ ሁኔታ ይቀርባል፡፡ ውይይት ይካሄዳል፡፡ በመጨረሻም ለመፍትሔ ጉዳይ የተግባር ኮሚቴ ተመርጦ፣ ይቋቋማል አሉን።  አቶ ሙሉጌታ ገብሩ የጄክዶ ሥራ አስኪያጅ ባደረጉት ንግግር ጥሪ የተደረገላቸውን እንግዶች  እንኳን ደህና መጣችሁ ካሉ በኋላ፤ “የኢየሩሣሌም ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት በ1984 ዓ.ም የሰሜኑ የአገራችን ክፍል የተፈጠረውን የአገራችን ችግር ለመፍታት የተመሠረተ ድርጅት መሆኑንና ህፃናትና ማህበረሰብ ላይ” እንደሚያተኩር ገልፀው፤ 5 ቅርንጫፍ መ/ቤቶች በብሾፍቱ፣ ድሬዳዋ፣ አዋሳ፣ አዳማ፣ ባህርዳርና ደብረ ብርሃን እንዳለውና በ18 የአገራችንንሰ ክፍሎች እንደሚንቀሳቀስ አስረድተዋል፡፡ ፕሮጀክቶቹ 1ኛ) ለትምህርት ለጤናና ወላጆቻቸውን ላጡ ህፃናት አገልግሎት ማስገኘት፤
2ኛ/የአየር ንብረት ለውጥ የአደጋ ቅነሳ (Climate Change እና disaster risk reduction) 3ኛ/ በአቅም ማጐልበት ዙሪያ እንሠራለን፡፡ ማህበራትን ማጐልበት፡፡
በ1983 በብሾፍቱ ሥራ የጀመርን ይመስለኛል፡፡ ለብሾፍቱ ዕድገት የበኩላችንን አስተዋጽኦ ያደረግን ይመስለኛል፡፡ የሥራችን አንዱ አቅጣጫ ማህበራዊ ተጠያቂነት ነው፡፡ 2008-2009 ይሄንኑ ሂደት በብሾፍቱ ዙሪያም አካሂደናል፡፡ ባካሄድነው ሂደት በአገልግሎት ሰጪው (መንግሥት) እና በአገልግሎት ተቀባዩ (ህዝብ) መካከል ፍፁም ቀናነትና መልካምነት የተመላ ስብሰባ አካሂደናል፡፡ ችግሮችን አንጥሮ በማውጣት ለጋራ መፍትሔ መሄዳችን ይታወሳል፡፡ ለአብነት ብሾፍቱን መጥቀስ ተገቢ ነው። በ2002 ብሾፍቱ ተጨማሪ ገቢ ነበረውና ይሄን ገቢ የከተማው አገልግሎት ለትምህርት እንዲውል ወስኖ ብሾፍቱ ላይ 70 ተጨማሪ መምህራን ተቀጠሩ፡፡
ከመንግሥት ሐላፊዎች ተቀባይነት አግኝቶ እንዲያውም ይሄንን ሂደት ወደሌሎች ሴክተሮች ብንወስደው ሸጋ ነው አልን - አገልግሎት ለመስጠት።
ወደሌሎች ከተሞች የሄድነው ብሾፍቱ ላይ በተነሳ ሀሳብ ነበር፡፡ ተሞክሮውን መነሻ በማድረግ እኤአ 2013 እና 14 ድርጅታችን የማህበረሰቡ በውሃ፣ ትምህርት እና አካባቢ ንፅህና ላይ አተኮረ። በሌሎችም የሀገሪቱ ክፍሎች ተንቀሳቀስን፡፡ ስለሆነም በዛሬው ዕለት በምናካሂደው ስብሰባ፤ አገልግሎት ተቀባይና ሰጪው በየበኩላቸው ችግር ብለው የለዩዋቸውን ጉዳዮች በጋራ የሚወያዩበት መድረክ ይሆናል ማለት ነው፡፡
ገፅ ለገፅ ማለት ይሄው ነው! Interface meeting፡፡ ሃሳባችንን ኃላፊነት በተሞላበትና ቅንነት ባለው መልኩ በመግለፅ ውጤታማ እንድናደርገው በአክብሮት እጠይቃለሁ፡፡
የሀገራችን የዲሞክራቲክ ሂደትና የመልካም አስተዳደር አንዱ ገጽታ ነው። ይሄ ዓይነት ውይይት ሠለጠን የሚሉትም ሀገሮች  የሚያካሂዱት አይደለም፡፡ ስለዚህ ይሄ ልዩ ያደርገዋል።
ቅን መንፈስና የጋራ መግባባት ውጤታማ እንደሚያደርገን ተስፋ አደርጋለሁኝ፡፡” ብለው ደምድመዋል፡፡
ቀጥሎ፤ ህዙቡስ ምን አለ? (ይቀጥላል)

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 24 May 2014 14:37

ራስ - በራስ - ለራስ

አገራችሁን የአፍሪካ ቀንድ ሳይሆን
የአፍሪካ ጭንቅላት ማድረግ እየቻላችሁ አላደረጋችሁም”

እውነት እውነት እላችኋለሁ… በምድር ላይ እንዲህ ያለ ቦታ አለ ብሎ ሰው ቢነግረኝ፣ ከቶውንም አላምንም ነበር፡፡ አልጠብቅማ! አልገምትማ! ምክንያቱም እንዲህ አድርጎ መስራት የሚችል ፈጣሪ ብቻ መሆኑን ስለማምን ነው፡፡
አንድርው መንደር ትባላለች፡፡ በካናዳ፣ በኞቫ ስኮሽያ ክ/ሃገር የምትገኝ መንደር ናት፡፡ የሃገራችን ከተሞች አንድ ቀበሌ ያህል ህዝብ ይኖርበታል፡፡ አንድርው መንደር፣ አረንጓዴ ስጋጃ የተነጠፈበት የሚመስል መልክዓ ምድር ያላት ሲሆን ሊኖሩባቸው ቀርቶ ሊዳብሷቸው የሚከብዱ መኖሪያና መስሪያ ቤቶች ያሉባት፣ ሁሉ በእጄ ሁሉ በደጄ የሆነባት ምድራዊት ገነት ነች፡፡ በመንደሩ ውስጥ ያሉ የውሃ፣ የመብራት፣ የትምህርት፣ የጤና፣ የመዝናኛ፣ የማህበራዊ መስተጋብር ወዘተ… አገልግሎቶች በፈጣሪ ተሰናድተውና ተቀናጅተው፣ በሰው እጅ ለሰዎች የሚቀርቡ ይመስላሉ፡፡ ከመንደሩ ለምነት የተነሳ የሚተነፈሰው አየር፣ ከኦክስጅንም በላይ የሆነ ኦክስጅን ነው፡፡ በጸደይ ወራት ፀሐይ ጨረሯን ሳታሳርፍበት ላስተዋለ አንድርው መንደር፣ በህብረ ቀለማት ከማሸብረቋ የተነሳ፣ በውስጧ የሚንቀሳቀሱ አናፍስት ሁሉ ከቶ የምድር አይመስሉም፡፡
በአንድርው መንደር ውስጥ ሆኜ ያደግሁበትን አካባቢ ሳስብ አነባሁ፡፡ በተለያዩ አጋጣሚዎች ተዘዋውሬ ያየኋቸውን የሀገሬን አካባቢዎችና መንደሬን ባሰብኩ ጊዜም ቆዘምኩ፡፡ በቦታው ድንቅነት፣ በማህበረሰቡ ኑሮ አይነፀሬነት በመደመም፣ ስለ አንድርው መንደር ለማወቅ ጓጓሁና ወደ አንድ የ71 ዓመት አዛውንት ጠጋ አልኩኝ፤ ራሴንም አስተዋወቅኋቸው፡፡ እሳቸውም ኢትዮጵያን ቀድመው ያውቋት ነበርና “ሀበሻ ነሃ!” አሉኝ፤ እኔም የሃበሽነት ወኔዬ መጣና “እንዴታ!” አልኳቸው፡፡
ፈገግ ብለው “ያች ሃገር ተለውጣለች ማለት ነው… ኮራ ብለህ እንዴታ የምትለኝ?” ሲሉኝ፣ ቅስሜ ስብር አለ፡፡ የተለመደ ቁስሌን ሊነኩት እንደሆነ ገብቶኛል፡፡ “ኢትዮጵያን የማውቃት ያልተገባትን ድህነት ወድዳና ፈቅዳ የለበሰች፣ በዚህ የድህነት ልብሷም የምትመካ ሃገር ሳለች ነበር፡፡ ይሄ ነገር ተቀይሯልን?!” አሉኝ፤ በጥርጣሬ ስሜት ተሞልተው፡፡
አዛውንቱ፤ በጠየቁኝ ጥያቄ የተነሳ፣ ጸጉሮቼ ሲቆሙ፣ አንዳንዶቹም ሲሰባበሩ በማስተዋላቸው  “ሀበሻ፤ የእኔውን ተወውና ወዳንተ ጥያቄ እንግባ” አሉኝ፡፡ እኔም እንደምንም ስሜቴን ለማረጋጋት ሞከርኩኝና፤
“አባት፤ ይህን መንደር ፈጥሮና አሰናድቶ የሰጣችሁን ፈጣሪ አግኝቼው በተማጸንኩትና የኢትዮጵያን መንደሮች በሙሉ እንዲህ ባደረገልኝ” አልኳቸው፡፡ እሳቸውም ፈገግ አሉና፤ “መንደሩን የሰራውና እንዲህ የምታየውን አይነት ኑሮ እንድንኖር ያደረገው ሰው የሚሉት ፍጡር ነው፡፡ አዎ! እኛው ራሳችን ነን እንዲህ አድርገን የሰራነው፡፡” ሲሉ መለሱልኝ፡፡
አዛውንቱ የሚሉትን አምኖ ለመቀበል ስለከበደኝ፤ “አምላክ ሆይ፤ እባክህ አለማመኔን ገስፀው” አልኩና “እንዴት?” አልኳቸው፡፡
“ይህ አካባቢና እኛው ራሳችን ከዓመታት በፊት በጠኔ፣ በርዛት፣ በተመጽዋችነት፣ በበልቶ አላዳሪነት፣ በበይ ተመልካችነት ….ነበር የምንኖረው። ከጊዜያት በኋላ ግን በተወሰኑ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ተነሳሽነት፣ የአካባቢን ሃብት መሰረት ያደረገ የማህበረሰብ ልማት ስራ ውስጥ ገባን፡፡ አየህ! በተለመደው መንገድ ችግሮቻችን ከመለየትና ድጋፍ ፍለጋ ከመሄድ ይልቅ ጥንካሬዎቻችንንና መልካም አጋጣሚዎቻችንን በሙሉ ለየን፡፡ የማህበረሰባችንን አጠቃላይ ተሰጥኦዎች በሙሉ ነቅሰን አወጣን፡፡ የማህበረሰቡ አባላትን ክህሎቶችና ችሎታዎች በሙሉ ዘረዘርን፤ በአካባቢያችን ያሉ ልንጠቀምባቸው የምንችላቸውን ማናቸውንም ነገሮች በሙሉ ለየን፡፡ እናማ በጊዜ ሂደት ያለማንም ድጋፍ በራሳችን አነሳሽነት፣ በራሳችን ቀያሽነት፣ በራሳችን አስተዳዳሪነት፣ በራሳችን ውሳኔ ሰጭነት፣ የራሳችንን ማለትም የማህበረሰባችንን ህይወት ቀየርነው፤ ራስ በራስ ይሏል ይህ ነው፡፡
“ዛሬ ድፍን ካናዳ እየመጣ ተሞክሯችንን ይጋራል፣ መንግስት፣ ዩኒቨርሲቲዎችና የሲቪል ማህበራቱም የእኛን ሞዴል በመጠቀም የተለያዩ አካባቢዎችን ቀይረዋል፤ እየቀየሩም ነው፡፡”
“ሀበሽ! ይህ መንደር ልጆች በታላቅ ስነ ምግባር፣ በእምቅ እውቀትና ክህሎት የሚታነጹበት፣ ወጣቶች ለሌሎች አርአያ በመሆን የሚወደሱበት፣ … የመሬት ገነት ነው፡፡”
እኔም በአካል አንድርው መንደር ሆኜ በህሊና ሀገር ቤት ስለነበርኩ “የሚያውቋትን ኢትዮጵያ ለማሻሻል ምን ማድረግ ይቻላል?” አልኳቸው፡፡
“አይ ሀበሻ! እናንተ እኮ ባላችሁ ዕምቅ ማህበረሰባዊ እሴት ከማንም ቀድማችሁ ማደግ የነበረባችሁ ህዝቦች ናችሁ፡፡ አየህ! እኛ እርስ በርሳችን አንተዋወቅም፡፡ የሚያገናኘን ማህበረሰባዊ እሴትም ልል ነው፡፡ ነገር ግን መሻቱ ስላለ፤ መንደርን፣ ክ/ሀገርን ብሎም ሀገርን ቀይረናል።
እናንተ ግን ጠንካራ ማህበራዊ ትስስር፣ በርካታ የማህበረሰብ አውታሮች እንዲሁም ተሰፍሮና ተለክቶ የተሰጠ አየር ንብረት፤ ሊሰራ የሚችል ትኩስ ጉልበት እያላችሁ፣ ሀገራችሁን የአፍሪካ ቀንድ ሳይሆን የአፍሪካ ጭንቅላት ማድረግ ሲገባችሁ አላደረጋችሁም፡፡ ስማ በዚያ ላይ በቅኝ ገዥዎች ላይ ድል የተቀዳጃችሁ ታላቅ ታሪክ ያላችሁ ህዝቦች ናችሁ፡፡ ያላችሁን አስተባብራችሁ ችጋርን ድል መንሳት ግን አልቻላችሁም፡፡
“ስማ ሀበሻ! ለእንዲህ አይነት በጎ ስራ ሁሉም ሰው በአንድ ላይ ላይነሳ ይችላል፡፡ ጥቂት ሰዎች ብቻ ተነሳሽነቱን ቢወስዱ ሁሉም ይቻላል፤ ጥቂት ሰዎች ሀገርን ይቀይራሉና፡፡
ተነሳሽነቱ፣ ታታሪነቱ፣ ትጋቱ፣ የእኔ ባይነቱ፣ ቅንነቱ፣ ዓላማው፣ ሩቅ አሳቢነቱ፣ መተሳሰቡ፣ ከራስ በፊት የማህበረሰብ ጥቅምን ማስቀደሙ ወዘተ… ካላችሁ፣ የራሳችሁን ምድራዊ ገነት መፍጠር ትችላላችሁ፡፡ ለሀበሻ ምድር ብቻ ሳይሆን ለሌሎች ዓላማት የሚበጁ ዜጎች የማፍራት ዕድሉ በእጃችሁ ነው…” እያሉ እያወጉኝ ሳለ፣ ሰዓት አልቋል የሚል ፊሽካ ከወደ አስተባባሪዎች ተነፋና ትቼአቸው ሄድኩ፡፡

Published in ህብረተሰብ