ህብረት ባንክ ለሚያስገነባው ባለ 32 ፎቅ ህንፃ፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ንግድ ስራ ኮሌጅ ፊት ለፊት በሚገኝ ቦታ ላይ የመሰረት ድንጋይ ተጣለ፡፡
የባንኩን ዘመናዊ ህንፃ ዲዛይን ለማድረግ ከ40 በላይ የኪነ-ህንፃ ባለሙያዎች የተወዳደሩ ሲሆን ህንፃው ባለ 4 ደርዝ የምድር ውስጥ የመኪና ማቆሚያ እንደሚኖረው ተገልጿል፡፡
ከትናንት በስቲያ የመሰረት ድንጋይ የመጣል ስነ-ስርአት ላይ ንግግር ያደረጉት የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ ታዬ ዲበኩሉ፤ ባንኩ ከእለት ወደ እለት በሁሉም ረገድ እያደገ መምጣቱን ጠቅሰው፤ የራሱን ዋና መስሪያ ቤት ህንፃ ማስገንባቱ በህብረተሰቡ ዘንድ የገነባውን መልካም ስምና ዝና ወደ ላቀ ደረጃ እንዲያሸጋግር ያግዘዋል ብለዋል፡፡
በስነ-ስርአቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኘው አትሌት ኃይሌ ገብረሥላሴ በበኩሉ፤ ባንኩ በግሉ ሴክተር የተሰማሩ ባለሀብቶችን በመደገፍ ከሚያደርገው ዘርፈ ብዙ ጥረት ጎን ለጎን አቅሙን በከፍተኛ ሁኔታ እያሳደገ መሆኑን ጠቁሞ፣ ህንፃው መገንባቱ የሚጠበቅና አስፈላጊም ጭምር ነው ብሏል፡፡  

Published in ዜና

ከኦስትሪያ የሚመጡት አሰልጣኝ በቀን 28 ሺ ብር ይከፈላቸዋል

ለዳቦና ኬክ ምርቶች ጥሬ እቃዎችን በማቅረብ የሚታወቀው ዴልታ የማምረቻና የንግድ ኩባንያ፤ የኢትዮጵያ የዳቦና የኬክ ሼፎችን በውጭ ባለሙያ ሊያሰለጥን እንደሆነ ተገለፀ፡፡ ከኦስትሪያ ቪየና የሚመጡት የዳቦና የኬክ ሥራ አሰልጣኝ ሚስተር ገንተር ኮክሲደር፤ በቀን 28 ሺህ ብር እንደሚከፈላቸው ታውቋል፡፡
ስልጠናው የሚሰጠው በክልልና በአዲስ አበባ የሚገኙ ሆቴሎች ለሚልኳቸው የዳቦና የኬክ ሼፎች ሲሆን በሀርመኒ ሆቴል በሚሰጠው ስልጠና ላይ በቀን 30 ሼፎችን በነፃ ለማሰልጠን መዘጋጀታቸውን የዴልታ ኩባንያ ባለቤትና ስራ አስኪያጅ አቶ አደም ሙዲ ገልፀዋል፡፡ ከ10 አይነት በላይ በሆኑ የኬኮችና የዳቦ አይነቶች አሰራር ላይ የሚሰጠው ስልጠና፤ በአገራችን የሚመረተውን የኬክና የዳቦ የጥራት ደረጃ በማሳደግ፣ ከየትኛውም አለም ለሚመጡ ሰዎች የሚመጥን እንዲሆን ያስችላል ተብሏል፡፡
ዴልታ ኩባንያ፤ የኬክና የዳቦ ምርቶችን ጥራት ባለው ደረጃ ለማምረት የሚስችል ፋብሪካ እየገነባ እንደሆነ የጠቆሙት አቶ አደም፤ ፋብሪካው የስልጠና ማዕከል እንደሚያካትትም ገልፀዋል፡፡ ከፍተኛ ገንዘብ አውጥተው ሥልጠና ለመስጠት ምን እንዳሳሰባቸው የተጠየቁት የዴልታ ኩባንያ ባለቤትና ሥራ አስኪጅ አቶ አደም ሲመልሱ፤ “ከውጭ የምናስገባቸው ለኬክና ለዳቦ ምርት የሚውሉ ጥሬ እቃዎች ጥሩ ሙያተኞች ጋ ካልደረሱ እኛ ዋጋ እናጣለን፤ ለዚህ ነው ባለሙያዎችን ለማሰልጠን የወሰንነው” ብለዋል፡፡ ስልጠናው የተዘጋጀው ጥሬ እቃ ከውጭ ከሚልኩላቸው ድርጅቶች ጋር በመተባበር እንደሆነም ጨምረው ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

ለበርካታ አመታት በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ሰፋፊ የምግባረ ሰናይ ስራዎችን በመስራት የሚታወቀው ‘ሰዎች ለሰዎች’ (Menschen für Menschen) የበጎ አድራጎት ድርጅት መስራች ኦስትሪያዊው በጎ አድራጊና ታዋቂ የፊልም ተዋናይ ካርልሀይንስ በም፣ ከትናንት በስቲያ በ86 አመታቸው አረፉ።
ባለፈው አመት የአልዛይመር በሽታ ተጠቂ መሆናቸው በይፋ የተነገረ ሲሆን ህክምናቸውን ሲከታተሉ ቆይተው፣ ከትናንት በስቲያ ምሽት በኦስትሪያ ከሳልዝቡር አቅራቢያ በምትገኘው ግሮዲግ ከተማ፣ በመኖሪያ ቤታቸው ህይወታቸው ማለፉን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
እ.ኤ.አ በ1928 ጀርመን ዳርምስታድ ውስጥ የተወለዱት ካርልሀይንስ በም፣ በስነጥበብ ታሪክና በትወና ትምህርታቸውን የተከታተሉ ሲሆን ለረጅም አመታት በፊልም ትወና ሙያ ተሰማርተው በርካታ ስራዎችን አከናውነዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ1981 ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት ‘ሰዎች ለሰዎች’ (Menschen für Menschen) የተባለውን የበጎ አድራጎት ድርጅት በመመስረትና በመምራት፣ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ብዙዎችን ተጠቃሚ ያደረጉ ከትምህርት፣ ከጤናና ከሌሎች ዘርፈ ብዙ ጉዳዮች ጋር የተያያዙ ስራዎችን በማከናወን ይታወቃሉ፡፡
‘ሰዎች ለሰዎች’ን ለረጅም ጊዜያት ሲመሩ የቆዩት ባለቤታቸው ወ/ሮ አልማዝ፣ ካለፈው ታህሳስ ወር ጀምሮ ድርጅቱን የማስተዳደሩን ሃላፊነት ለሌሎች አስረክበው ወደ ኦስትሪያ በመሄድ ባለቤታቸውን ሲያስታምሙ እንደነበር  እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡  
በበጎ አድራጎት ስራቸው ላከናወኑት የላቀ አስተዋጽኦ የኢትዮጵያ መንግስት በ1995 ዓ.ም የክብር ዜግነት የሰጣቸውና ሳር ቤት ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በስማቸው አደባባይ  ተሰይሞ ሃውልት የቆመላቸው ካርልሀይንስ፣ ታዋቂዎቹን የ‘ባላንዛ የሰብዓዊነት፣ የሰላምና የወንድማማችነት ሽልማት’ እና ‘ኢሴል የማህበራዊ አስተዋጽኦ ሽልማት’ ጨምሮ፤ ከተለያዩ አገራት በርካታ የስኬትና የአገልግሎት ሽልማቶችን አግኝተዋል፡፡
ካርልሀይንስ ‘ሲሲ’፣ ‘ፎክስ ኤንድ ሂዝ ፍሬንድስ’፣ ‘ላ ፓሎማ’፣ ‘ዘ ስቶው አዌይ’ እና ‘ካም ፍላይ ዊዝ ሚ’ን ጨምሮ፤ በአሜሪካ፣ በጀርመን፣ በኦስትሪያና በሌሎች አገሮች በተሰሩ 45 ያህል ፊልሞች ላይ በመተወን ችሎታቸውን ያስመሰከሩ ተዋናይ መሆናቸውን ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር ዘግቧል፡፡
በ1983 ዓ.ም ከኢትዮጵያዊቷ ባለቤታቸው አልማዝ ተሾመ ጋር በመሰረቱት ትዳር ሁለት ልጆችን ያፈሩት ካርልሀይንስ በም፤ ከቀድሞ ትዳሮቻቸው ያፈሯቸው አምስት ልጆች አሏቸው፡፡

Published in ዜና

ጳጳሳት የፓትርያርኩን የማኅበረ ቅዱሳን ደንብ ማሻሻያ ቅድመ ኹኔታ አልተቀበሉትም
‹‹ቅድመ ኹኔታው የማኅበሩን አገልግሎት የሚያቀጭጭና በሒደትም የሚያስቆም ነው›› /ታዛቢዎች/

የማኅበረ ቅዱሳን መተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅን እንደ አንድ አጀንዳ የያዘው የዘንድሮው የሲኖዶሱ የርክበ ካህናት ጉባኤ ከረቂቁ ጋር በተያያዘ በፓትርያርኩና በሊቃነ ጳጳሳቱ መካከል በተፈጠረ ፍጥጫ መጠናቀቁ ተገለጸ፡፡
የፍጥጫው መንሥኤ፣ በቅዱስ ሲኖዶሱ የተሠየመው የማኅበረ ቅዱሳን መተዳደርያ ደንብ አጥኚ ኮሚቴ ያዘጋጀው የማሻሻያ ረቂቅ በዝርዝር ከመታየቱ አስቀድሞ ፓትርያርኩ ለውይይቱ እንደ ቅድመ ኹኔታ ያቀረቧቸው ነጥቦች በአብዛኛው የጉባኤው አባላት የገጠመው ተቃውሞ እንደኾነ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የቅ/ሲኖዶሱን ስብሰባ በርእሰ ጉባኤነት የሚመሩት ፓትርያርኩ፤ በአጀንዳው ላይ የሚካሔደውን ውይይት ቀጣይነት ይወስናል በሚል ካቀረቧቸው ቅድመ ኹኔታዎች ውስጥ÷ ለአጥኚ ኮሚቴው መመሪያ የሰጡባቸው ‹‹ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችና ግዴታዎች›› አንድም ሳይቀነሱ በደንቡ እንዲካተቱና ረቂቁ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ከጸደቀ በኋላ እንዲታይ የሚሉ እንደሚገኙበት ተመልክቷል፡፡
ፓትርያርኩ በቅድመ ኹኔታ አስቀምጠዋቸዋል በተባሉት ነጥቦች ስምምነት ላይ ከተደረሰ ስብሰባው ሊቀጥል እንደሚችል በመጥቀስ፣ ኃይለ ቃልም ተማኅፅኖም በተቀላቀለበት አኳኋን መጠየቃቸው ተዘግቧል፡፡
ይኹንና የሚበዙት ሊቃነ ጳጳሳት በቀጥታ እንደተቃወሟቸው፣ የተቀሩትም ድጋፍ ከመስጠት እንደተቆጠቡ ታውቋል፡፡ ፍጥጫው ቀጥሎ አቡነ ማትያስ ‹‹አቋሜ ይኽው ነው፤›› በሚል አጀንዳውን መዝጋታቸውን ሲያስታውቁም፣ ‹‹የማኅበረ ቅዱሳን ጉዳይ እንዲህ ተብሎ የሚተው አይደለም፤›› በሚል ከኹሉም ሊቃነ ጳጳሳት ጠንካራ ተቃውሞ እንደገጠማቸው ምንጮች ይገልፃሉ፡፡
የቅ/ሲኖዶሱ መደበኛ ስብሰባ የሚካሔደው ምልዓተ ጉባኤው ከጅምሩ ተስማምቶ ባጸደቃቸው የመነጋገርያ አጀንዳዎች መሠረት እንደኾነ በሊቃነ ጳጳሳቱ ተቃውሞ ተጠቅሷል፡፡
የማኅበሩ የመተዳደርያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅ እንዲቀርብ ከታዘዘበት ከጥቅምት 2005 ዓ.ም. ጀምሮ እየተንከባለለ ለኹለት ዓመታት መዘግየቱን ሊቃነ ጳጳሳቱ አስታውሰው፣ የተጓተተው አጀንዳ ‹‹የማኅበሩን አገልግሎት ያቀጭጫሉ፣ በሒደትም ያስቆማሉ›› በሚል በተተቹት የፓትርያርኩ ቅድመ ኹኔታዎች ሊዘጋ እንደማይችልና ተጨማሪ ጊዜ ሳይወስድ ቅ/ሲኖዶሱ ሊወያይበት እንደሚገባ በአጽንዖት በመናገራቸው፣ ጉዳዩ ሳይቋጭ ለቀጣዩ ቀን በይደር ተላልፏል፡፡
አጀንዳው ሰኞ፣ ግንቦት 18 ቀን 2006 ዓ.ም. ጥዋት መታየት ሲጀምር፣ አጥኚ ኮሚቴው በ37 አንቀጾችና በ34 ገጾች አሻሽሎ ያዘጋጀው የማኅበሩ መተዳደርያ ደንብና የኮሚቴው ቃለ ጉባኤ በንባብ መሰማቱም ታውቋል፡፡ ፓትርያርኩ ‹‹ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችና ግዴታዎች›› በሚል ራሱን በቻለ ርእስ በደንቡ እንዲካተት ለአጥኚ ኮሚቴው ጥብቅ መመሪያ የሰጡበት ባለ24 አንቀጽ ሰነድም አብሮ እንዲነበብላቸው መጠየቃቸው የመጀመሪያው ቀን የፍጥጫ መነሻ እንደነበር ታውቋል፡፡
በ24 አንቀጾችና በአምስት ገጾች የተዘረዘሩት የፓትርያርኩ ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችና ግዴታዎች÷ በአባላቱ በጎ ፈቃድ ተቋቁሞ ከፍተኛ አስተዋፅኦ በማበርከት ላይ የሚገኘውን ማኅበር፤ ከሕገ ተፈጥሮው ውጭ የሚያደርግ፣ በቅ/ሲኖዶሱ ፈቃድ ከሚመራበት ደንብ በተፃራሪ ተቋማዊ ህልውናውን፣ የአመራር ምርጫውን፣ የአባላት አያያዙንና የሥራ ቦታውን ለውጭ ተጽዕኖ አሳልፎ የሚሰጥና አጣብቂኝ ውስጥ የሚያስገባ፣ በአርኣያነት የሚጠቀሰውን የፋይናንስ አሠራሩን ወደ ኋላ የሚጎትት መኾኑን እንደተረዱ ያብራሩ አንድ የቅ/ሲኖዶሱ አባል፣ ‹‹ቀጣዩ ቀንም የከበደ ነገር ይዞ እንደሚመጣ ግልጽ ነበር፤›› ይላሉ፡፡
በይደር የተያዘው አጀንዳ በቀጣዩ ቀን ማክሰኞ ጥዋት ተጀምሮ ለግማሽ ቀን የቀጠለ ቢኾንም ፓትርያርኩና ሊቃነ ጳጳሳቱ የመተዳደርያ ደንብ ማሻሻያውን በዝርዝር ለመመልከት የሚያስችል ስምምነት ላይ ለመድረስ እንዳልቻሉ ታውቋል፡፡
‹‹ፓትርያርኩ በቅድመ ኹኔታ ያስቀመጧቸውን ነጥቦችና በአጀንዳው ቀጣይነት ላይ የያዙትን አቋም አልቀየሩም፤ ሊቃነ ጳጳሳቱም ባጸደቅነው አጀንዳ መሠረት ቅድሚያ ሰጥተን መነጋገር ያለብን የሠየምነው አጥኚ ኮሚቴ አዘጋጅቶ ባቀረበው ረቂቅ ላይ ነው፤ መካተት ያለበት ነገር ካለም ማኅበሩን በሚያሠራ መልኩ እያገናዘብን በሒደት እናየዋለን እንጂ አጀንዳው በቅድመ ኹኔታ መታሰር የለበትም በሚል ለማስረዳት ጣሩ፤ በመጨረሻም ፓትርያርኩ “እንግዲያውስ ስብሰባውን ለመምራት አልችልም” በማለታቸው የስብሰባው መቋጫ ኾኗል፤›› ይላሉ- ሒደቱን ለአዲስ አድማስ የገለጹ የስብሰባው ምንጮች፡፡
የማኅበሩ ደንብ በመጀመሪያ ረድፍ ከሰፈሩት የቅ/ሲኖዶሱ መነጋገርያ ነጥቦች አንዱ እንደነበር ያስተዋሉ ሌሎች የስብሰባው ተከታታዮች በበኩላቸው፤ አጀንዳው ከቅደም ተከተሉ ወጥቶ እየተገፋ በመጨረሻ መነሣቱ በፓትርያርኩና በሊቃነ ጳጳሳቱ መካከል ይህ ዓይነቱ አለመግባባት ሊነሣ እንደሚችል ጠቋሚ ነበር ብለዋል፡፡  
ተከታታዮቹ አክለውም፣ ፓትርያርኩ ስብሰባውን ለመምራት ፈቃደኛ ባይኾኑም በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ በተደነገገው የቅ/ሲኖዶስ ስብሰባ ሥነ ሥርዓት መሠረት፣ ምልዓተ ጉባኤው በማኅበሩ መተዳደርያ ደንብ ማሻሻያዎች ላይ የጀመረውን ውይይት ቀጥሎ ውሳኔ ለማሳለፍ የሚችልባቸው አግባቦች እንደነበሩ ገልጸው፣ ቅ/ሲኖዶሱ በግለጫው የመጨረሻው አጀንዳው ባደረገው የማኅበሩ ደንብ ላይ “ውይይት ተደርጎበታል” ከማለት በስተቀር ስብሰባውን የቋጨበት አኳኋን ያልተለመደና አደናጋሪ ነው ብለዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን የዘመኑን ኦርቶዶክሳዊ ትውልድ አደራጅቶ ማንነቱን የሚያውቅበትንና በግብረ ገብ የሚታነፅበትን ትምህርተ ሃይማኖት ከማስተማር ባሻገር፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማት አገልግሎታቸውን በብቃት የሚወጡበትን ኹለገብ ሞያዊ ድጋፍ የመስጠት ሓላፊነት እንዳለበት በደንብ አጥኚ ኮሚቴው ማሻሻያ ረቂቅ ላይ መስፈሩ ታውቋል፡፡
ይኹንና ‹‹ጥበቃና ጥንቃቄ›› በሚል ፓትርያርኩ እንደ መመሪያ ያቀረቧቸው ድንጋጌዎችና ግዴታዎች እንዲሁም ከልዩ ጽ/ቤታቸው ማኅበሩን አስመልክቶ በየጊዜው የሚወጡ መመሪያዎች የማኅበሩን አገልግሎት የማቀጨጭ፣ በሒደትም አዳክሞ የማስቆም ውጤት ሊኖራቸው እንደሚችል ታዛቢዎች ያስረዳሉ፡፡
የማኅበሩ መተዳደርያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅ፣ ቅ/ሲኖዶሱ የማኅበሩ ደንብ እንዲሻሻል ግንቦት 14 ቀን 2004 ዓ.ም. ባካሔደው ስብሰባ÷ ማኅበሩ ከጊዜው ጋር የሚሔድ፣ አገልግሎቱና አደረጃጀቱ የደረሰበትን ስፋትና ዕድገት የሚመጥን፣ ለቤተ ክርስቲያን ኹለንተናዊ ልማት የሚጠቅም ድርጅታዊ መዋቅር እንደሚያስፈልገው ባሳለፈው ውሳኔ መሠረት አምስት ሊቃነ ጳጳሳት፣ ገለልተኛ የሕግ ባለሞያዎችና የማኅበሩ አባላት በታከሉበት አጥኚ ኮሚቴ የጋራ ጥናት የተዘጋጀ መኾኑ ተመልክቷል፡፡
በግንቦት ወር 1984 ዓ.ም. በበጎ ፈቃድ በተሰበሰቡ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የተመሠረተው ማኅበሩ፤ እየተመራ ያለው ቅ/ሲኖዶስ በ1994 ዓ.ም. ለሦስተኛ ጊዜ አሻሽሎ በሰጠው መተዳደርያ ደንብ ሲኾን አሁን የተሻሻለው ረቂቅ ተመርምሮ ባለመጽደቁ በነባሩ ደንብ እየተመራ ለመቀጠል እንደሚገደድ ተመልክቷል፡፡

Published in ዜና

          “ትዝ ይለኛል… ዕለቱ ማክሰኞ ነበር፡፡ ማለዳ ላይ የኢትዮጵያ ሬድዮ፤ ኢህአዴግ አገሪቱን መቆጣጠሩንና የመንግስት ለውጥ መደረጉን መናገሩ አካባቢያችን የፍርሃት ድባብ አጥልቶበታል፡፡ ት/ቤታችንም ከተዘጋ ቀናት ተቆጥረዋል፡፡ በዚህ ምክንያትም ቤተሰቦቼ ከቤት እንድወጣ አይፈቅዱልኝም ነበር፡፡ ቤት መቀመጥ በጣም ቢሰለቸኝም አማራጭ አልነበረኝም፡፡ ከቤታችን በራፍ ላይ ባለችው ገላጣ ሜዳ ላይ የሰፈር ልጆች ለጥቂት ደቂቃዎች ሰብሰብ ብለን የቆምን እንደሆነ ‘ተበተኑ’ የሚል ፈጣን ትእዛዝ ይደርሰናል፡፡ ያኔ እንዲህ እንዳሁኑ ቴሌቪዥንም ሆነ ሌሎች መዝናኛ ነገሮች እንደልብ ባለመኖራቸው እቤት እምንውልበት ጊዜ በጣም አሰልቺ ነው፡፡ በአካባቢያችን የሚገኙ በርካታ የመንግስት ተቋማት እየተሰበሩ ይዘረፉ ነበር፡፡ ፈጥኖ ደራሽ እየተባለ የሚጠራው የፖሊስ ማሰልጠኛ ማእከል ከተዘረፈ በኋላ አብዛኛው የሰፈራችን ነዋሪ ባለመሳሪያ ሆነ፡፡ የማሰልጠኛው እቃ ግምጃ ቤት ተሰብሮ የተዘረፈ እለት ከዘራፊዎቹ መካከል እርስ በርስ ተታኩሰው የሞቱ የሰፈር ልጆችም ነበሩ፡፡ በርካታ አዳዲስና ያገለገሉ የተለያዩ አይነት የጦር መሳሪያዎች፣ በንጉሱ ጊዜ ለማሰልጠኛው የተገዙ የተለያዩ ውድ እቃዎችና የጦሩ አልባሳት በዘራፊዎቹ ከመወሰዳቸውም በላይ ለጦሩ ደመወዝ የመጣ በሚሊዮን የሚቆጠር ጥሬ ገንዘብ የዘራፊዎች ሲሳይ ሆኗል፡፡ ግርግርና እረብሻ በአካባቢያችን የተለመደ ጉዳይ ነበር፡፡

አብዛኞቻችን (የሰፈራችን ሰዎች) ቤተሰቦች ስለሆንን የነበረው ውጥረት ከሌሎች አካባቢዎች ሁሉ በእኛ መንደር የባሰ ይመስለኛል፡፡ ቤተሰቦቼ ወደ እነዚህ የረብሻና የዘረፋ ቦታዎች እንድሄድ ፈፅመው አይፈቅዱልኝም፡፡ ለቤቱ ብቸኛ ወንድ እኔ በመሆኔም፣ ከሴቶቹ ይልቅ በእኔ ላይ ጠንከር ያለ ቁጥጥር ይደረግብኝ ነበር፡፡ የኢህአዴግ ሰራዊት ከተማውን በይፋ መቆጣጠሩ በሬድዮን ከተነገረ በኋላ፣ ሁኔታዎች ይበልጥ እየተለወጡ ሄዱ፡፡ ግንቦት 19 ምሽትና ሌሊቱን ከሆለታ መስመር ወደ አዲስ አበባ ከገባው የኢህአዴግ ሰራዊት ጋር የመንደራችን ወጣቶች ተጋጭተው፣ አንድ ወጣት ከኢህአዴግ ታጋይ በተተኮሰ ጥይት ህይወቱን አጣ፡፡ አባቴ በማግስቱ ከጥቂት የሰፈራችን ሰዎች ጋር ወጣቱን ለመቅበር ወደ ፊሊጶስ ቤተክርስቲያን ሄደ፡፡ እኔም እግሩን ተከትዬ ከቤት ወጣሁ፡፡ የሰፈሬ ልጆች፣ የሸጎሌ ጥይት ማምረቻና ማከማቻ መጋዘን ተሰብሮ እየተዘረፈ እንደሆነና ወደዚያው ሊሄዱ መሆኑን ነገሩኝ፡፡ ከእነሱ ጋር ሄጄ ሁኔታውን የማየት ጉጉት አደረብኝ፡፡

ለቀናት በቤተሰቦቼ የተነፈግሁትን ነፃነት በአጋጣሚ በማግኘቴ፣ ሳልጠቀምበት እንዲያመልጠኝ አልፈለግሁም፡፡ ታዲ፣ ስዩም፣ ፈቃዱ፣ ዮሐንስ፣ ዘካርያስ፣ ግሩሜ፣ አሌክስና እኔ ስምንት ሆነን ወደ ስፍራው ጉዞ ጀመርን፡፡ ሁላችንም እድሜያችን ከ18 ዓመት በታች ነበር፡፡ ወደ ስፍራው እየተቃረብን ስንሄድ ምድር ቀውጢ ሆናለች፡፡ በየሜዳው የተበታተኑ የጥይት ቀለሆች፣ የተቀዳዱ ካርቶኖች በብዛት ይታያሉ፡፡ የዊንጌትን ዳገታማ መንገድ ጨርሰን በስፍራው ስንደርስ በሜርኩሪ ዘረፋ ላይ ነበሩ የተባሉ ሰዎች በጥይት ሲታኮሱ በማየታችን እጅግ ፈራን፤ ግን ሁኔታውን ለማየትና ከተገኘም የተራረፈ ነገር ለመለቃቀም አስበን ተጠጋን፡፡ ሁላችንም አንድ ላይ እንድንሆንና እንዳንለያይ ተነጋግረን ነበር፡፡ ትዝ ይለኛል ሰዓቱ ወደ ምሳ ሰዓት አካባቢ ነው፡፡ ወደ ስፍራው ተጠግተን ጥቂት እንኳን ሳንቆይ አካባቢውን የሚነቀንቅ ኃይለኛ ፍንዳታና የእሳት ብልጭታ ከአንድ ስፍራ ተነሳ፡፡ ከዛ በኋላ ምኑን ልንገርሽ… ምድር ቀውጢ ሆነች፡፡ እዚህም እዚያም ሃይለኛ ፍንዳታና ጩኸት ብቻ ሆነ፡፡

ካየሁ ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ግን የሆነውን አላውቅም፡፡ ራሴን ያወቅሁትና የነቃሁት ከ32 ቀናት በኋላ ባልቻ ሆስፒታል ውስጥ ነበር፡፡ በሆስፒታሉ ለ4 ወራት ባደረግሁት ህክምና ህይወቴ ከሞት ቢተርፍም ዘላቂ አካል ጉዳተኛ ከመሆን አልዳንኩም፡፡ በደረሰብኝ አደጋ የጀርባዬና የፊቴ ግማሽ ክፍል እንዲሁም የግራ እጅና እግሬ ስጋዎች ሙልጭ ብለው ተገፈዋል፡፡ በጭንቅላቴ ላይ ፀጉር የሚባል ነገር አልነበረም፡፡ በሚገባ መንቃቴንና ራሴን ማወቄን የተገነዘቡት ቤተሰቦቼ በደረሰብኝ ጉዳት እንዳላዝንና እንዳልከፋ፤ ይልቁንም በህይወት በመትረፌ መደሰት እንደሚገባኝ እየነገሩ እንድፅናና ያበረታቱኝ ጀመር፡፡ ከሰፈራችን ተጠራርተን አብረን ከሄድነው ስምንት ጓደኞቼ መካከል በህይወት የተረፍኩት እኔ ብቻ ነበርኩ፡፡ ሰባቱ ዘግናኝ በሆነ ሁኔታ ህይወታቸውን እንዳጡ ተነገረኝ፡፡ የደረሰብኝን የጉዳት መጠን ሳየው በሞቱት ጓደኞቼ ቀናሁ፡፡ በባልቻ ሆስፒታል አራት ወር ሙሉ ፍዳዬን አየሁ፡፡ ሀኪሞቹ የተበላሸውን የፊት ገፅታዬን ለመመለስ ያደረጉት ጥረት በጥቂቱም ቢሆን ተሳክቶላቸዋል፡፡ ከመቀመጫዬና ከእግሬ እየተወሰደ በፊቴና በአንገቴ ላይ በተለጣጠፉት ስጋዎቼ ሰው መምሰል ቻልኩ፡፡

በአጋጣሚ እኔን ያክመኝ የነበረው ሩሲያዊ ወጣት ዶ/ር፣ ወደ ሀገሩ ለእረፍት ሄዶ ሲመለስ፣ የፊቴን ቆዳ ለማስተካከል የሚረዱ ቅባቶችና መድኃኒቶች ይዞልኝ መጣ፡፡ ይህን ፊቴን የተሻለ ለማድረግ በእጅጉ ጠቅሞኛል፡፡ በባልቻ ሆስፒታል ቆይታዬ ወደተኛሁበት ክፍል እየመጡ አደጋው በደረሰብኝ ስፍራ ላይ ያገኘሁትን ሜርኩሪ በውድ ዋጋ እንደሚገዙኝ እየነገሩ የሚያግባቡኝ ፈረንጆች ነበሩ፡፡ እኔ ግን እንኳንስ ሜርኩሪ ላገኝ ቀርቶ፤ በቦታው እየተካሄደ የነበረው ምን እንደሆነ እንኳን በቅጡ ሳይገባኝ ነበር ለአደጋ የተጋለጥኩት፡፡ ከሆስፒታሉ ከወጣሁኝ በኋላ ከአንድ አመት በላይ ከቤቴ ተኝቼ ህክምናዬን ስከታተል ቆይቻለሁ፡፡ በዚህ ምክንያትም ትምህርቴ ለሁለት ዓመት ተቋርጧል፡፡ ቀስ በቀስ አደጋው ያደረሰብኝ የአካል እና የአእምሮ ጉዳት እየቀነሰ ሄዶ ሳገግም፣ ትምህርቴንም ካቆምኩበት ቀጠልኩና አሁን ላለሁበት ደረጃ ልደርስ ቻልኩ፡፡ ግንቦት 20 በመጣ ቁጥር ግን የደረሰብኝ አደጋና እስከ ወዲያኛው ያጣኋቸው ጓደኞቼ ትዝ ይሉኛል፡፡ ለእኔ የግንቦት 20 ፍሬዬ የአመታት ህመምና ስቃይ እንዲሁም አካል ጉዳተኝነት ነው፡፡” ይህንን ያለኝ በአንድ ስመ ገናና ኤንጂኦ ውስጥ በኃላፊነት ደረጃ ተመድቦ በመስራት ላይ የሚገኝና የ37 ዓመት ጎልማሳ የሆነው ፍፁም ኃ/ኢየሱስ ነው፡፡ ፍፁም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በኢኮኖሚክስ ሁለተኛ ዲግሪውን በከፍተኛ ማዕረግ አጠናቆ ከተመረቀ አምስት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ በተማረበት የትምህርት መስክ በተለያዩ ድርጅቶች ለዓመታት ሰርቷል፡፡ አሁን በሚሰራበት መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ውስጥ ጠቀም ባለ ደመወዝ ከተቀጠረ ሁለት ዓመት አልፎታል፡፡

ምንም እንኳን ኑሮው የተደላደለ ቢሆንም ውስጡ ደስተኛ እንዳልሆነ ይናገራል፡፡ የብቸኝነት ስሜት ያሰቃየዋል የፊት ገፅታውን ለመመለስ መስዋዕትነትን የከፈሉት መቀመጫው፣ ዳሌውና የእግሩ ባቶች በጨርቅ ካልሆነ በስተቀር ለእይታ ሊያጋልጣቸው እንደማይደፍርም አውግቶኛል፡፡ በአደጋው ከደረሰበት የአካል ጉዳት ቢያገግምም የአእምሮው ጉዳቱ ግን እያደር እየባሰበት እንደሄደና ኑሮውን የብቸኝነትና የሰቀቀን እንዳደረገበት አልሸሸገኝም፡፡ ለም ሆቴል እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ተገንብተው ለከተማዋ ውበት ከሰጡት ህንጻዎች አንዱ ባለቤት ነው፡፡ ግንቦት 20 ቀን 1983 ዓ.ም በሸጎሌ የጥይት ማምረቻና ማከማቻ መጋዘን ላይ በደረሰው የፍንዳታ አደጋ ጉዳት ከደረሰባቸው ሰዎች መካከል አንዱ ነው፡፡ በአደጋው ግራ እጁንና አንድ አይኑን አጥቶ በህይወት ለመትረፍ ችሏል፡፡ ወደ ሥፍራው የሄደው ከሶስት ጓደኞቹ እና ከታላቅ ወንድሙ ጋር ቢሆንም በህይወት የተመለሱት እሱና አንድ አብሮ አደግ ጓደኛው ብቻ ነበሩ፡፡ ቴዎድሮስ (ለፅሁፉ ስሙ የተቀየረ) ከአደጋው ያተረፈው አካል ጉዳተኝነቱን ብቻ አልነበረም፤ ህይወቱን ለመቀየር ያስቻለውን ሀብቱን ጭምር ነበር፡፡

መኖሪያ ቤታቸው በጥይት ፋብሪካው አካባቢ በመሆኑ መጋዘኑ ተሰብሮ ዘረፋው ሲጀመር ከስፍራው ከደረሱት ጥቂት ሰዎች መካከል አንዱ እሱና ጓደኞቹ ይገኙበታል፡፡ ከልጅነታቸው ጀምሮ ሲወራ ይሰሙ የነበሩትንና ከመጋዘኑ ህንፃ በታች (አንደር ግራውንድ) ውስጥ የተቀበረና ለጥይት ማምረቻው የሚያገለግል ሜርኩሪ የተባለው ማዕድን ይገኝበታል የተባለውን ስፍራ የቅድሚያ ኢላማቸው አደረጉት፡፡ እንደሀሳባቸው ሆኖም ውድ ማዕድኑ ያሉበትን ቦታ በማግኘታቸው ዕድል የሰጣቸውን አፍሰው ወጡ፡፡ ያገኙት ማዕድን እጅግ ውድ ዋጋ እንደሚያወጣ ሲነገራቸው፣ ተጨማሪ የማግኘቱ ጉጉት አደረባቸውና በድጋሚ ወደስፍራው አመሩ፡፡ ሆኖም ለሁለት ጓደኞቹና ለታላቅ ወንድሙ ሞትን፣ ለእሱ ከፍተኛ የአካል ጉዳትን እንጂ ተጨማሪ ሜርኩሪን አላስገኘላቸውም፡፡ ቴዎድሮስ በአሁኑ ወቅት የ47 ዓመት ጎልማሳ ነው፡፡ “ዛሬ በሆነ አጋጣሚ አደጋው በደረሰበት ስፍራ ላይ በተሰራ የቀለበት መንገድ በመኪና ሳልፍ ያኔ የነበረው ሁኔታና ድርጊቱ ሁሉ አሁን የተፈፀመ ያህል ይታየኛል፡፡ ግንቦት 20 ለእኔ ዝብርቅርቅ ያለ ስሜትን የሚፈጥርብኝ ቀን ነው፡፡ እውነቱን ተናገር ካልሽኝ፣ እለቱ ፍፁም ባይታወስና ባይከበር ደስ ይለኛል፡፡” አለኝ ስሜቱ ተረብሾ፡፡ ወ/ሮ ሽታዬ ሰሙንጉስ በሸጎሌው አደጋ ሶስት ልጆቻቸውን ያጡ እናት ናቸው፡፡ በ18፣በ16ና በ12 ዓመት እድሜ ክልል ውስጥ የነበሩት ሶስት ወንዶች ልጆቻቸው ወሬ እንመልከት ብለው ከቤት እንደወጡ በዛው መቅረታቸውን ነግረውኛል፡፡

ሁለቱ ልጆች እዛው አደጋው በደረሰበት ስፍራ ህይወታቸውን ሲያጡ፣ አንደኛው ልጃቸው ግን ለአንድ ወር በባልቻ ሆስፒታል ህክምና ሲደረግለት ከቆየ በኋላ፤ ህይወቱ አልፏል፡፡ ወ/ሮ ሽታዬ፤ በእለቱ የነበረውን ሁኔታ ሲያስታውሱት አይኖቻቸው በእንባ ይሞላሉ፡፡ ለረባ ቀብር እንኳ ያልታደሉት ልጆቻቸውን በከፋ ችግርና እንግልት ማሳደጋቸውንና ልጆቹም በባህሪያቸው አስቸጋሪዎችና ረባሾች እንዳልነበሩ ይናገራሉ፡፡ “በአንድ ጀንበር ከወላድነት ወደ መካንነት ተሸጋግሬ በህይወት መኖር መቻሌ እንኳንስ ለተመልካች ለእኔም ትንግርት ነው፡፡ ግን ላያስችል አይሰጥ አይደል እሚባለው? ይኸው የሰጠኝን በፀጋ ተቀብዬ 23 ዓመት ለመኖር ችያለሁ፡፡ አደጋው የደረሰ ሰሞን እራሴን ሁሉ ስቼ ነበር፤ እራሴን ለማጥፋትም ብዙ ሙከራ አድርጌያለሁ ግን አልሆነልኝም፡፡ ፈጣሪ ለምን እንደፈለገኝ ባላውቅም ይኸው ቁጭ አድርጎኛል፡፡ አንድ ጊዜ በቀበሌያችን በተደረገ ስብሰባ ላይ ተገኝቼ አደጋው ለደረሰባቸው ሰማእታት ለምን ሀውልት በቦታው ላይ አይሰራም ብዬ ብጠይቅ፣ አንዱ የቀበሌያችን ተመራጭ ‹ልጆችሽ ያለቁት እኮ ለአገራቸው ደህንነት ሲታገሉ አይደለም፤ መጋዘን ሰብረው ሲዘርፉ ነው› አለኝ፤ ምን እላለሁ? “እኔን ሆነህ እየው” ብዬው ወጣሁ፡፡ ይኸው 23 ዓመት ሙሉ ግማሽ ህይወቴን እኖራለሁ፡፡

አሁን ግንቦት 20 ምኑ እሚያስደስት ቀን ሆኖ ነው… በዚህ ሁሉ ቸበርቻቻና በዚህ ሁሉ ግርግር የሚከበረው፤ እለቱ ያመጣብን መዓትና መከራንና ችግርን ብቻ ነው፡፡” ወ/ሮ ሽታዬ የልጆቻቸው ሀዘን ዛሬም የወጣላቸው አይመስሉም አይኖቻቸው በእንባ ብዛት እየሟሙና እየደከሙ መሄዳቸው ያስታውቃል፡፡ ዛሬም በእነዚሁ አይኖቻቸው ያነባሉ፡፡ ኑሮዋቸው ተስፋና ጉጉት አልባ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ እንደሳቸው ሁሉ በእለቱ በደረሰው የፍንዳታ አደጋ ህይወታቸውን ባጡ ልጆቻቸው ኑሮዋቸው በሀዘንና ሰቀቀን የተሞላ በርካታ እናቶች ሸጎሌ እና አካባቢዋን በከፋ ሀዘን ያስታውሱታል፡፡ የዛሬ 23 ዓመት ግንቦት 20 ከቀኑ 5 ሰዓት ከ45 ደቂቃ ላይ በደረሰው የፍንዳታ አደጋ፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች ህጻናትና ጎልማሶች ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡ በአደጋው ለአካል ጉዳት የተዳረጉ ታዳጊዎችና ህፃናት፣ ወጣቶችና ጎልማሶችም ቤት ይቁጠራቸው፡፡ አካባቢው ለወራት በመጥፎ ሽታና በአሞራዎች ተወርሮ ነበር፡፡ ዛሬ አካባቢው ታርሶ በተገነቡ ቤቶች ውስጥ በርካታ ነዋሪዎች ሰፍረውበታል፡፡ ከዊንጌት አዲሱ ገበያ ድረስ የሚዘልቀው የቀለበት መንገድ የተሰራውም በዚሁ ፍንዳታ በደረሰበት ቦታ ላይ ነው፡፡ የሸጎሌውን ፍንዳታና በፍንዳታው ህይወታቸውን ያጡ ወገኖችን የሚያስታውስና እንደ ወ/ሮ ሽታዬ ያሉ እናቶችን የሚያፅና ምንም ነገር በስፍራው የለም፡፡

Published in ህብረተሰብ

በ800 ሜትር ሳይሸነፍ 15 ወራት አልፈዋል
ዘንድሮ ለዳይመንድ ሊግ ድል ለሃትሪክ ተጠብቋል
አዲስ የዓለም ሪከርድ እንደሚያስመዘግብ ግምት ተሰጥቶታል

አትሌት መሃመድ አማን ባለፉት 15 ወራት በሮጠባቸው የ800 ውድድሮች አልተሸነፈም፡፡ ኢትዮጵያ በዓለም የአትሌቲክስ ስፖርት ላለፉት 30 ዓመታት በረጅም ርቀት ከፍተኛ ስኬት ያስመዘገቡ አትሌቶችን በማፍራት ትታወቅ ነበር፡፡ ባለፉት 5 ዓመታት ግን በ20 ዓመቱ የዓለማችን የመካከለኛ ርቀት ምርጥ ሯጭ  ኮርታለች፡፡ አትሌት መሃመድ የኢትዮጵያን የአትሌቲክስ ዝና በአዲስ ምዕራፍ ቀይሶታል፡፡
ዘንድሮ በዳይመንድ ሊግ ውድድሮች ላይ ምርጥ ብቃት ያሳያሉ ተብለው ከተጠበቁ ምርጥ አትሌቶች አንዱ የሆነው መሃመድ በዚህ የውድድር ዘመን የ800 ሜትር የዓለም ሪከርድን ሊሰብር እንደሚችል በመገመትም ላይ ነው፡፡  በእርግጥም በርቀት አይነቱ  የዓለም ንጉስ ለመባል የሚቀረው ሪከርዱን መስበር ብቻ ነው፡፡ አንዳንድ የአትሌቲክስ ባለሙያዎች አትሌቱ አሁን በያዘው ብቃት ከቀጠለ ዘንድሮ ባይሳካለት እንኳን በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት በዓለም አቀፍ ውድድሮች የሚኖሩት ልምዶች የዓለም ሪከርድን የሚያሻሽልበት ብቃት ላይ እንደሚያደርሱት እየመሰከሩ ናቸው፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት የ2014  የዳይመንድ ሊግ ውድድር በኳታር ዶሃ ሲጀመር አንፀባራቂ ከነበሩ አትሌቶች ዋናው የነበረው አትሌት መሃመድ አማን፤ በወቅቱ በ800 ሜትር ውድድር ሲያሸንፍ ያሳየው አስደናቂ የአጨራረስ ብቃት ከፍተኛ አድናቆት አጉርፎለታል፡፡ እንደውም አንዳንድ ዘገባዎች ‹‹ሱፕር አትሌት›› ብለው አግንነውታል፡፡ ይሁንና አትሌቱ ከ2013 አጋማሽ ጀምሮ በተሳተፈባቸው የ800 ሜትር ውድድሮች ሳይሸነፍ ለመቆየቱ በቂ ምክንያት በማቅረብ የሚከራከሩ አልጠፉም፡፡ በእነዚህ ተከራካሪዎች መሃመድ አማን የሚቀናቀነው የጠፋው በተለይ የርቀቱ ሁለት ምርጥ አትሌቶች ጋር ባለመገናኘቱ ነው የሚል ማስረጃ ይቀርባል፡፡ በ2012 እኤአ ላይ ለንደን ኦሎምፒክ ላይ የዓለምን ሪከርድ ያስመዘገበው የ25 ዓመቱ ኬንያዊው ዴቪድ ሩዲሻ በጉዳት ከውድድር ከራቀ ሁለት ዓመት አልፎታል፡፡ ሌላው ምርጥ አትሌት እና በእድሜው እኩያው የሆነው ደግሞ የቦትስዋናው ኒጄል አሞስ ሲሆን እሱም በጉዳት ከውድድር እንደራቀ ነው፡፡
በዓለም አትሌቲክስ ዘንድሮ በከፍተኛ ጉጉት ከሚጠበቁ ትንቅንቆች ዋንኛው መሃመድ አማን ፤ ኒጄል አሞስ እና ዴቪድ ሩዲሻ የሚገናኙበት የ800 ሜትር  ፍጥጫ እንደሆነ ይገለፃል፡፡ ሶስቱ አትሌቶች በዳይመንድ ሊግ መገናኘታቸው እየተጠበቀ ሲሆን በተለይ ከሳምንት በኋላ በአሜሪካዋ ከተማ ዩጂን፤ የሚደረገው የፕሮፎንታይኔ ክላሲክስ ላይ ከተገናኙ አስገራሚ ፉክክር እንደሚኖራቸው   ተገምቷል፡፡ የ800 ሜትር የዓለም ሪከርድ በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር በኦፊሴላዊ ደረጃ መመዝገብ የተጀመረው በ1952 እኤአ ነው፡፡ የመጀመርያው ሪከርድ በአሜሪካዊው አትሌት ቴድ ሜሪንዴዝ በ1.51 ደቂቃዎች የተመዘገበ ሲሆን ከዚሁ ሪኮርድ በኋላ 24 ጊዜ ሰዓቱ ሲሻሻል በርካታ እንግሊዛዊያንና አሜካዊያን አስተዋኝኦ ነበራቸው፡፡ ከ2008 ጀምሮ የተመዘገቡ ሦስት ሪኮርዶችን ማስመዝገብ የቻለው ኬንያዊው ዴቪድ ሩዲሻ ሲሆን የወቅቱ ሪከርድ ከ2 ዓመት በፊት በለንደን ኦሎምፒክ  በ1 ደቂቃ ከ41.54 ሰኮንዶች ያስመዘገበው ነው፡፡ አትሌት መሃመድ አማን ዘንድሮ በርቀቱ ሪከርድ ለመስበር  ፍላጐት እንዳለው በይፋ የተናገረው ነገር ባይኖርም የራሱን ምርጥ ሰዓት ወይንም የኢትዮጵያን ሪከርድ ለ7ኛ ጊዜ ለማሻሻል ያስባል፡፡ 800 ሜትርን ከ1.40 ደቂቃ በታች እንደሚገባም ያምናል፡፡

ምርጥ ሰዓቶቹ- በ800 ሜትር 1፡42.37 ቤልጅዬም ብራሰልስ  በ2013 እኤአ የተመዘገበ ሰዓት ሲሆን የኢትዮጵያ ሪከርድ ነው፡፡ በ800 ሜትር የኢትዮጵያ ሪከርድን ለስድስት ጊዜያት አሻሽሏል፡፡ በ1500 ሜትር 3፡43.52 ምርጥ ሰዓት ያስመዘገበ ሲሆን በ1 ማይል ያለው ምርጥ ሰዓት ደግሞ 3፡57.14 ነው፡፡
ወቅታዊ ደረጃው- በኦልአትሌቲትክስ ድረገፅ ዘንድሮ በ800 ሜትር በ1405 ነጥብ የዓለም አንደኛ አትሌት ሲሆን በሁሉም የአትሌቲክስ የውድድር መደቦች በተመሳሳይ ነጥብ ከዓለም 8ኛ ነው፡፡ በዓለም የ800 ሜትር የምንግዜም ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ 9ኛ ነው፡፡
ማኔጅመንት እና ስፖንሰር -የትጥቅ ስፖንሰሩ ናይኪ ሲሆን፤ ከ2009 እኤአ ጀምሮ ኤሊት ስፖርትስ ማኔጅመንት ኢንተርናሽናል ESMI በመታቀፍ እየሰራ ነው፡፡
አስደናቂ ድሎቹ- አሁን በጉዳት ላይ የሚገኘው የኬንያው አትሌት ዴቪድ ሩዲሻ የ800 ሜትር የዓለም ሪከርድን ለስድስት ጊዜያት አሻሽሏል፡፡ ግዙፉ አትሌት በሩጫ ዘመኑ ካደረጋቸው 47 ውድድሮች 45ቱን አሸንፏል፡፡ የተሸነፈባቸው ሁለት ውድድሮች የመሃመድ አማን ሁለት አስደናቂ ድሎች ናቸው፡፡ የመጀመርያው በ2011 እኤአ ላይ በጣሊያኗ ከተማ ሬቲ ያሸነፈበት ሲሆን በወቅቱ ዴቪድ ሩዲሻ ለመጀመርያ ጊዜ የተሸነፈው ከ34 ተከታታይ ድሎች በኋላ ነበር፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በ2012 እኤአ ላይ በዙሪክ የተካሄደ የዳይመንድ ሊግ ውድድር ሲሆን በዚህ ወሳኝ ትንቅንቅ ለመጀመርያ ጊዜ የዳይመንድ ሊግ ዋንጫን ያሸነፈበት ነበር፡፡

በእግር ኳስ ዓመታዊ ትርፍ 2.8 ቢሊዮን ዶላር የአዲዳስ 1.9 ቢሊዮን ዶላር የናይኪ
አዲዳስና ናይኪ ዓለም ዋንጫው ገና ወራት ሲቀሩት በገበያ ዘመቻቸው ከባድ ትንቅንቅ ውስጥ ገብተዋል፡፡ ሁለቱ ኩባንያዎች በእግር ኳሱ የማልያ ትጥቅ አቅራቢነት ከ5 ቢሊዮን ዶላር በላይ በየዓመቱ ያንቀሳቅሳሉ፡፡ በከፍተኛ የቴክኖሎጂ እገዛ የተመረጡ ታኬታዎችና ማልያዎችን በማቅረብ ፉክክራቸውን ያጧጡፋሉ፡፡
ናይኪ ለዓለም ዋንጫው ያቀረበው ታኬታ የቅርጫት ኳስና የሩጫ ጫማዎች የተሰሩባቸውን ቴክኖሎጂ አጣምሮ የያዘው “ማጂስታ” ነው፡፡ ኢኒዬስታና ማርዮ ጎትዜ በዚህ ታኬታ አሠራር ላይ የሃሳብ ተሳታፊ ነበሩ፡፡ የናይኪ “ማጂስታ” ታኬታ ዋጋ 275 ዶላር ነው፡፡ አዲዳስም “አዲዜሮ ኤፍ50” በሚል ስያሜ በሊዮኔል ሜሲ የሚተዋወቁትን የታኬታ ምርቶች ለዓለም ዋንጫው ይዞ ቀርቧል፡፡ የገበያ ዋጋቸው 270 ዶላር አካባቢ ነው፡፡የዓለም ዋንጫዋን ኳስ “ብራዙካ” ያቀረበውም አዲዳስ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት የዓለማችን ግዙፉ የስፖርት ትጥቅ አምራች ኩባንያ በዓለም ገበያ 17% ድርሻ የያዘውና 25 ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ ገቢ ያስመዘገበው የአሜሪካው ናይኪ ነው፡፡ የጀርመኑ ኩባንያ አዲዳስ በ12% የገበያ ድርሻ እና በ20 ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ ገቢ ይከተለዋል፡፡
አዲዳስ  ከዓለም ዋንጫ ውድድሮች እና በአጠቃላይ በእግር ኳስ ስፖርት የቅርብ አጋር ሆኖ ሲሰራ ከ66 ዓመታት በላይ አስቆጥሯል፡፡ በአንፃሩ ናይኪ ከዓለም ዋንጫ እና ከእግር ኳስ ስፖርት ጋር መንቀሳቀስ ከጀመረ ገና 20 ዓመቱ ነው፡፡
በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ላይ ናይኪ የ10 ብሔራዊ ቡድኖችን ትጥቅ ሲያቀርብ የአዲዳስ 9 ናቸው፡፡ ፑማ ለ8 ብሔራዊ ቡድኖች ትጥቅ በማቅረብ 3ኛ ደረጃ አለው፡፡  
የዓለም ኮከብ ተጨዋች ክርስቲያኖ ሮናልዶ የናይኪ ታኬታዎች ዋና አምባሣደር ሲሆን የብራዚልና የፖርቱጋል ብሄራዊ ቡድኖች ሙሉ ትጥቅ ከሚወስዱት ይጠቀሳሉ፡፡  የስፔንና የጀርመን ብሔራዊ ቡድኖች ደግሞ የአዲዳስ ዋና ደንበኞች ሆነው ሲጠቀሱ በፊፋ የዓለም ኮከብ ተጨዋች ተብሎ ለ4 ጊዜያት የተመረጠው ሊዩኔል ሜሲ የአዲዳስ ትጥቆች ዋና አምባሳደር ነው፡፡ ፡፡
በኢንተርኔት የማህበረሰብ ድረገፆች በቀጠለው የሁለቱ ኩባንያዎች ዘመቻ ናይኪ ብልጫ ሲኖረው 36 ሚሊዮን የፌስ ቡክ ወዳጆች፣ እንዲሁም 8.8 ቢሊዮን የትዊተር ተከታታዮች በማስመዝገቡ ነው፡፡ አዲዳስ 17 ሚሊዮን የፌስ ቡክ ወዳጆች እና 9.4 ሚሊዮን የትዊተር ተከታታዮች አሉት፡፡

የዓለማችን የረጅም ርቀት ምርጥ አትሌቶች የሆኑት  ቀነኒሣ በቀለ እና ጥሩነሽ ዲባባ በጐዳና ላይ ሩጫዎች ስኬታማ እየሆኑ ናቸው፡፡  ባለፈው ሳምንት  በእንግሊዝ በተካሄደው የቡፓ ግሬት ማንቸስተር ራን በ10 ኪ.ሜ የጐዳና ላይ ሩጫ በሁለቱም ፆታዎች አሸናፊ ሆነዋል፡፡
አትሌት ቀነኒሣ በቀለ በወንዶች ምድብ ያሸነፈው ርቀቱን በ28.23 ደቂቃዎች በመሸፈን ነበር፡፡ የዓለም ማራቶን ሪኮርድ ባለቤቱን ኬንያዊው ዊልሰን ኪፕሳንግ በ5 ሰኮንዶች በመቅደም አስከትሎት ገብቷል፡፡ ይህ ውጤት  ሁለቱ አትሌቶች ለመጀመርያ  በማራቶን የሚገናኙበትን ሁኔታ አጓጊነት ጨምሮታል፡፡ ዊልሰን ኪንሳንግ በ2013 አጋማሽ ላይ በበርሊን ማራቶን 2 ሰዓት ከ03 ደቂቃ ከ23 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ  የዓለም ሪከርድን ያስመዘገበ ነው፡፡ ከወር በፊት ቀነኒሳ የመጀመርያ ማራቶኑን በፓሪስ ሮጦ የቦታውን ሪከርድ አስመዝግቦ ሲያሸንፍ በዚያው ሰሞን ዊልሰን ኪፕሳንግም በለንደን ማራቶን በተመሳሳይ የቦታውን ሪከርድ አስመዝግቦ ማሸነፉ ይታወሳል፡፡ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ በቀጣዩ የውድድር ዘመን ከዊልሰን ኪፕሳንግ ጋር በማራቶን መሮጥ ፍላጎት እንዳለውም የሰጠው፡፡ ከቡፓ ግሬት ማንችስተር ራን በኋላ ቀነኒሳ በሰጠው አስተያየት አሁን ትኩረቱ ወደ ትራክ ውድድሮች መመለስ እንደሆነ ገልፆ፤ በተለይ በ10ሺ ሜትር አንድ ውድድር ማድረግ እንደሚፈልግ አስታውቋል፡፡ በሌላ በኩል በሴቶች ምድብ ደግሞ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ ርቀቱን በ32 ደቂቃ ከ20 ሰኮንዶች በመሸፈን አሸንፋለች፡፡ ጥሩነሽ  በቡፓ ግሬት ማንችስተር ራን ዘንድሮ ያሸነፈችው ለሁለተኛ ግዜ  ሲሆን አምና ውድድሩን ስታሸንፍ በ30.49 ደቂቃዎች በሆነ ጊዜ የቦታውን ሪከርድ አስመዝግባ ነበር ፡፡
ከወር በፊት በፓሪስ እና ለንደን በተካሄዱ የማራቶን ውድድሮች የመጀመርያ ማራቶናቸውን የሮጡት ቀነኒሳ በቀለ እና ጥሩነሽ ዲባባ አጀማመራቸው ስኬታማ እነደሆነ ያመለከቱ መረጃዎች፤ በሚቀጥሉት ዓመታት በሁለቱም ፆታዎች የተያዙ የዓለም ማራቶን ሪከርዶችን ለመስበር ግንባር ቀደም እጩዎች ስለመሆናቸውም ግምት ሰጥተዋል፡፡ የመጀመርያ ማራቶኑን በፓሪስ የሮጠው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ የቦታውን ሪከርድ ካሸነፈ በኋላ ያሳየው ብቃት በሚቀጥሉት 5 ዓመታት የዓለም ማራቶን ሪከርድን ሊሰብር እንደሚችል ያመለክታል በሚል በርካታ ዘገባዎች አውስተውለታል፡፡ አትሌት ቀነኒሳ የፓሪስ ማራቶንን ሲያሸንፍ ርቀቱን የሸፈነበት 2 ሰአት ከ05 ደቂቃ ከ4 ሰኮንዶች ነበር፡፡ በረጅም ርቀት 5 የዓለም ሻምፒዮና እንዲሁም 3 የኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳልያዎች ያሏት ጥሩነሽ ዲባባ ደግሞ ከወር በፊት በለንደን የመጀመርያ ማራቶን ውድድሯን  በሁለት ሰዓት ከ20 ደቂቃ ከ54 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ በሶስተኛ ደረጃ ጨርሳለች፡፡ ይሄው የጥሩነሽ ሰዓት በማራቶን የመጀመርያ ሩጫ ከተመዘገቡ ፈጣን ሰዓቶች በሶስተኛ ደረጃ ተመዝግቧል፡፡

ሚድሮክ ኢትዮጵያ የአትሌቲክስ ክለብ ይመሠረታል
ሚድሮክ ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ግሩፕ በሚቀጥለው ዓመት የአትሌቲክስ ስፖርት ክለብ እንደሚመሰርት አስታወቀ፡፡  በሚድሮክ ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ስር ባሉ ኩባንያዎች መካከል ዘንድሮ ለ11ኛ ጊዜ የተካሄደው ዓመታዊ የስፖርት ውድድር ሰሞኑን ተጠናቅቋል፡፡ በዚሁ ዓመታዊ የስፖርት ውድድር መዝጊያ ስነስርዓት ላይ ንግግር ያደረጉት ዋና ስራ አስፈፃሚው ዶ/ር አረጋ ይርዳው የሚድሮክ ኢትዮጵያ የአትሌቲክስ ክለብ ለመመስረት የተወሰነው በስፖርቱ እድገት ላይ ተገቢውን  ድርሻ ለማበርከት ታቅዶ ነው ብለዋል፡፡ የመቻሬ የእግር ኳስ ክለብ ወደ ብሔራዊ ሊግ ደረጃ ለማድረስ ከፍተኛ ጥረት እንደሚያደርግም ዋና ስራ አስፈፃሚው ተናግረዋል።

       ዛሬ በፖርቱጋል ዋና ከተማ ሊዝበን በሚገኘው  ኢስታድዮ ዳ ሉዝ ስታድዬም ለ59ኛው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ  ዋንጫ  ሁለቱ የማድሪድ ከተማ ክለቦች ሪያልና አትሌቲኮ ማድሪድ  ይፋጠጣሉ፡፡ በሻምፒዮንስ ሊግ ታሪክ ለፍፃሜ ጨዋታ የአንድ ከተማ ክለቦች ሲገናኙ  ለመጀመርያ ጊዜ  ነው፡፡ የዋንጫ ጨዋታው በ200 አገራት የቀጥታ ቴሌቭዢን ስርጭት ሲኖረው እስከ 1 ቢሊዮን ተመልካች እንደሚያገኝ ተገምቷል፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ዋንጫውን ለሚያሸንፈው ክለብ 10.5 ሚሊዮን ዩሮ እንዲሁም ለሁለተኛው ክለብ ደግሞ 6.5 ሚሊዮን ዩሮ ያበረክታል፡፡ በአጠቃላይ ሁለቱ የማድሪድ ክለቦች እስከ ፍፃሜው በነበራቸው ግስጋሴ ከቴሌቭዥን ስርጭት መብት፤ ከሜዳ ገቢ እና ከተለያዩ ንግዶች በነፍስ ወከፍ እስከ 55 ሚሊዮን ዩሮ ድርሻ ይኖራቸዋል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ ከዋንጫው ጨዋታ በፊት በተደረጉት 124 ጨዋታዎች 357 ጎሎች ሲመዘገቡ፤ ኮከብ ግብ አግቢነቱን የሪያል ማድሪዱ ክርስትያኖ ሮናልዶ በ16 ጎሎች እየመራው ነው፡፡
ሁለቱ የማድሪድ ከተማ ክለቦች እርስ በራስ የሚገናኙበት ጨዋታ “ኤል ደርቢ ማድሪሊያኖ” በሚል መጠሪያ ሲታወቅ ከዛሬው የዋንጫ ጨዋታ በፊት  264 ጨዋታዎች ተደርገውበታል፡፡  በ143 ሪያል ማድሪድ ሲያሸንፍ በ64  ጨዋታዎች ያሸነፈው  አትሌቲኮ ማድሪድ ነው፡፡ በ57 ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይተዋል፡፡ ኤልደርቢ ማድሪሊያኖ አንድ ክፍል ዘመን ያስቆጠረ የእግር ኳስ ትንቅንቅ ነው፡፡  ባለፉት አስር ዓመታት ይህን ታላቅ ደርቢ ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና የሚገናኙበት ኤልክላሲኮ ሸፍኖት  ቆይቷል፡፡
 የዓለም ሃብታሙ ክለብ ሪያል ማድሪድ ዛሬ ዋንጫውን ካነሳ በውድድሩ ታሪክ ለ10ኛ ጊዜ ይሆናል፡፡ ከዚህ ቀደም 13 ጊዜ ለፍፃሜ ቀርቦ 9 ዋንጫዎችን ወስዷል፡፡ የመጨረሻው ድሉ ከ12 ዓመት በፊት ነው፡፡ በአንፃሩ አትሌቲኮ የሚያገኘው ድል በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ  ነው፡፡ ከ40 ዓመት በፊት ብቸኛውን የፍፃሜ ጨዋታ አድርጎ  በባየር ሙኒክ 5ለ0 ተሸንፎ ዋንጫውን አልምጦታል፡፡ ሪያል ማድሪድ ኮፓ ዴ ላሬይን ቢያሸንፍም የውድድር ዘመኑን ውጤታማ ለማለት የግድ የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ ያስፈልገዋል፡፡ ባለፈው ሳምንት   ከ18 ዓመት በኋላ  የላሊጋ ዋንጫን ላገኘው አትሌቲኮ የማድሪድ ከተማ በ200ሺ ደጋፊዎች ተጥለቅልቃ ነበር ፡፡ የአውሮፓን ክብር ደርቦ ካሸነፈ  ደግሞ በከተማዋ የሚኖረው ፌሽታ ሚሊዮኖችን ያሳትፋል ተብሏል፡፡
ሪያል ማድሪድ በአገር ውስጥ ውድድሮች ከ60 በላይ፤ በአውሮፓ ደረጃ ከ11 በላይ ዋንጫዎችን የሰበሰበ ሲሆን አትሌቲኮ  በአገር ውስጥ ውድድሮች 24 በአውሮፓ ደረጃ ደግሞ 5 ዋንጫዎች አሉት፡፡
በስፔን ፕሪሚዬራ ሊጋ ሪያል ማድሪድ  32 ጊዜ ሻምፒዮን ሲሆን አትሌቲኮ ዘንድሮ 10ኛውን የሻምፒዮናነት ክብር አግኝቷል፡፡ በኮፓ ዴላሬይ ሪያል ማድሪድ 19 ዋንጫ ሲወስድ አትሌቲኮ ማድሪድ 10 አለው፡፡ሪያል ማድሪድ ለውድድር ዘመኑ የነበረው በጀት 515 ሚሊዮን ዩሮ ሲሆን በ4 እጥፍ የሚያንሰው የአትሌቲኮ በጀት 120 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡
ሪያል ማድሪድ ማልያውን ከፍተኛ ስፖንሰርሺፕ ሲያገኝበት አትሌቲኮ ማድሪድ ለ2 የውድድር ዘመን ስፖንሰር አጥቶ የአዘርባጃን መፈክር ላንድ ኦፍ ፋየርን ለጥፎ ቅናሽ ገቢ አለው፡፡
ሪያል ማድሪድ  የተመሰረተው ከ112 ዓመታት በፊት ሲሆን በዘንድሮ አጠቃላይ የተጨዋቾች ስብስቡ በትራንስፈር ማርኬት 505 ሚሊዮን ዩሮ የዋጋ ተመን ሲኖረው  ከተመሰረተ ከ111 ዓመታት የሚሆነው የአትሌቲኮ ማድሪድ የተጨዋቾች ስብስብ ተመኑ 282 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡

Page 6 of 21