እንጀራ ሳይሻግት 10 ቀናት ማቆየት ተቻለ

የኢትዮጵያውያን ባህላዊ ምግብ ሲባል በአብዛኛው ትዝ የሚለን እንጀራ በወጥ ነው። ብዙ ሰዎች “እንጀራ ሳልበላ ሁለት ቀን መቆየት አልችልም” ሲሉ ይደመጣሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ደግሞ ለእንጀራ ደንታ የላቸውም፡፡ “ጭድ መብላት ሆድ መሙላት ነው፡፡ እንጀራ ባልበላ ከአይረን (ብረት ማዕድን) በስተቀር ምን ይቀርብኛል? ብረት እንደሆን ከሌላ ምግብ አገኛለሁ” ይላሉ፡፡ እነዚህ የእንጀራ ጥቅምና ምስጢር ያልገባቸው ናቸው ማለት ይቻላል፡፡ እንጀራ የሕልውና መሠረት ስለሆነ በኅብረተሰቡ ውስጥ ብዙ ባህላዊ አባባሎች አሉት። “እንጀራህ ይባረክ፤ ጥሩ እንጀራ ይስጣችሁ፤ ጥሩ እንጀራ ይውጣልሽ፣ የማታ እንጀራ ይስጥህ፣ ሌማታችሁ በእንጀራ ይሞላ፤ ከሌማትሽ የምትቆርሺው እንጀራ አትጪ፣…” እና የመሳሰሉት ናቸው፡፡ እንጀራ፣ ለበርካታ ዘመናት የኅብረተሰቡ ምግብ ሆኖ ቢቆይም በርካታ ችግሮች እንዳሉበት የታወቀ ነው፡፡ ለመሆኑ እንጀራ ሳይሻግት ስንት ቀን ይቆያል? ብልዎት መልስዎ “ሦስት ወይም አራት ቀን” እንደሚሆን አልጠራጠርም፡፡ ቶሎ መሻገቱ ዋነኛ ችግሩ ነው፡፡ ሌላው ደግሞ በመሻገቱ የተነሳ የሚፈጠረው ብክነት ነው፡፡

የሻገተ እንጀራ ስለማይበላ ይደፋል፤ ባከነ ማለት ነው፡፡ ልጆች ሆነን ታናሽ ወንድሜ የሻገተ እንጀራ ከተሰጠው፤ “ጢም ያወጣ እንጀራ አልበላም” ብሎ የሚያኮርፈው ትዝ ይለኛል፡፡ ዛሬ፣ እንጀራ ስላለው ጠቃሚ ነገሮችና ስለ አንድ የምርምር ውጤት አጫውታችኋለሁ፡፡ ምርምሩ የተካሄደው በአውሮፓ ወይም አሜሪካ አይደለም - እዚሁ በአገራችን ካሉት ቀደምት የትምህርት ተቋማት አንዱ በሆነው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ነው፡፡ የጥናቱ ውጤት እንጀራ ሳይሻግት 10 ቀናት ማቆየት የሚያስችል ነው። ውጤቱንም ያገኘው የውጭ ዜጋ አይደለም - ወጣት ኢትዮጵያዊ ተመራማሪ ነው፡፡ ተመራማው አቶ አሻግሬ ዘውዱ ይባላል። የምርምሩ ውጤት አንቱ የሚያሰኝ ቢሆንም ከዕድሜው ወጣትነት የተነሳ አንተ ልለው ተገድጃለሁ፡፡

አቶ አሻግሬ የተወለደው በአዲስ አበባ ከተማ ነው - በ1973 ዓ.ም፡፡ የመጀመሪያ ዲግሪውን ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲ በኬሚስትሪ አግኝቷል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በ “ፉድ ሳይንስ ኤንድ ኑትሪሽን ሴንተር” መምህርና ተመራማሪ ነው፡፡ ሁለተኛ ዲግሪውን ያገኘው እንጀራ ሳይሻግት ለብዙ ቀናት ማቆየት በሚቻልበት ዘዴ ላይ ባደረገው ምርምር ነው፡፡ ሦስተኛ ዲግሪውንም በእንጉዳይ ላይ ባደረገው ጥናት ለመያዝ ተቃርቧል፡፡ በእንጀራ ዙሪያ ባደረገው ጥናትና ለወደፊት በምን መልኩ ሊያቀርበው እንዳሰበ ከአቶ አሻግሬ ዘውዱ ጋር ያደረግሁት ቃለ - ምልልስ በዚህ መልኩ ቀርቧል፡፡

 በእንጀራ ላይ እንዴት ለመመራመር አሰብክ?

ለሁለተኛ ዲግሪዬ አአዩ ገብቼ ስማር ነው ሐሳቡ የመጣው፡፡ የማስተርስ ዲግሪ ለማግኘት ምርምር መሠራት አለበት፡፡ የእንጀራው ሐሳብ የመጣው ከአማካሪዬ ከዶ/ር ዳዊት አባተ ነው፡፡ ጥናትህን የአገራችን ችግር በሆነ ነገር ላይ ለምን አታደርግም? ለምሳሌ የፀሎታችንን መጀመሪያ “አባታችን ሆይ የዕለት እንጀራችንን ስጠን” የሚል ነው፡፡ ትላልቅ ሰዎችም ሲመርቁን ጥሩ እንጀራ ይስጥህ/ሽ ይላሉ። ለምን በእሱ ላይ አትሠራም? አሉኝ፡፡ እኔም ሐሳባቸውን ተቀብዬ በእንጀራ ላይ ለመሥራት ተስማማሁ፡፡

ከጥናቱ ምን አገኘህ?

እንጀራ ብዙ ችግሮች አሉት፡፡ አንደኛውና ዋናው ቶሎ ይሻግታል፡፡ ሌላው ደግሞ ብክነት ነው፡፡ ይኼ በየቤቱ ያለ ችግር ነው፡፡ ትምህርቱን የምንማረው ከውጭ ነው፡፡ እነሱ ምግቦቻቸው ሳይበላሹ እንዲቆዩ (ሼልፍ ላይፍ) የሚያደርጉት እንዴት ነው? በማለት ዘዴውን ማጥናት ጀመርን፡፡ የአሜሪካ የምግብና መድኃኒት ቁጥጥር ባለሥልጣን ኤፍዲ ኤ የፈቀዳቸው ዘዴዎች አሉ። ከዘዴዎቹ አንዱ ፕሪዘርቫቲቭ (Preservative) ነው። ይህ ዘዴ ማንኛውም ኬሚካል መጠኑን ከጠበቅህ፤ መርዛማ ሳይሆንና ሳይበላሽ መቆየት ይችላል የሚል ነው፡፡ ማንኛውም ነገር መጠኑ ከበዛ ውሃም ሆነ ስኳር ይበላሻል፤ መርዝ ነው፡፡ እነሱ ዳቦ ሳይበላሽ ብዙ ጊዜ እንዲያቆይ የሚያደርጉት ኬሚካሎችን መጥነው በመጨመር ነው፡፡

ለመሆኑ እንጀራ እንዲሻግት (እንዲበላሽ) የሚያደርገው ምንድነው?

እንጀራን የሚያሻግተው ፈንገስ ወይም ሞልድ (mould) ነው፡፡ መጠኑን ጠብቀን ያንን ፈንገስ የሚያጠፋ ኬሚካል ብንጨምርበት እንጀራውን ሳይበላሽ ሊቆይ ይችላል፡፡ እነሱ ዳቦ ሳይበላሽ የሚያቆዩትን በእንጀራ ላይ ሞክረነው እንጀራ ሳይበላሽ ከሦስት ቀን እስከ 10 ቀን እንዲቆይ ማድረግ ችለናል፡፡ ትልቁን ውጤት ያመጣው ቤንዞይክ አሲድ ይባላል፡፡ አንድ ነገር የአሲድነቱ መጠን ከፍ ቢል ጥቃቃን ሕዋሳት ማደግ አይችሉም፡፡ እንጀራ በተፈጥሮው ይኮመጥጣል፡፡ እንዲኮመጥጥ የሚያደርጉት ደግሞ አሲዶች ናቸው፡፡ ዱቄቱ በሚቦካበት ሂደት የሚፈጠሩ አሲዶች አሉ። የእነዚህ አሲዶች መፈጠር ወይም የእንጀራ መኮምጠጥ የሚጠቅመን ነገር አለው፡፡ ባክቴሪያ አያድግበትም፤ ፈንገስ ብቻ ነው ያንን አሲድነት ተቋቁሞ ሊያድግ የሚችለው፡፡ የጨጓራ ሕመም ያለበት ሰው አፍለኛ እንጀራ እንዲበላ የሚመከረው አሲድ ከመፈጠሩ በፊት ስለሚጋገር ነው፡፡ አፍለኛ እንጀራ ሲበላ አይኮመጥጥም - ይጣፍጣል፡፡ የሚጣፍጠው እንጀራው ሲጋገር የተፈጠረው ስኳር በመሆኑ ነው።

ውጤቱን ያገኛችሁት እንዴት ነው?

ኬሚካሉ የሚጨመረው ዱቄቱ ሲቦካ ነው? ወይስ ሊጡ ሲጋገር? በአገራችን አንድ ነገር ሲሠራ፣ ዳቦ ሲጋገርም ሆነ ጠላ ሲጠመቅ፣ ወጥ ሲሠራም ሆነ እንጀራ ሲጋገር፣ … መጨመር ያለባቸውን ነገሮች (ንጥረ-ነገሮች) ይህን ያህል መጠን ያለው ጨው ስኳር፣ በርበሬ፣ … መጠኑን ወይም ልኬቱን የሚወስን ሕግ የለም፡፡ ኅብረተሰቡ የሚጠቀመው በልምድ ነው፡፡ አሁን ግን ለሁሉም ነገር መጠን እንዲወጣ ከኢትዮጵያ ጥራትና ደረጃዎች ባለሥልጣን ጋር እየሠራን ነው፡፡ እኛ የተጠቀምነው የአሜሪካን የምግብና መጠጥ ቁጥጥር ባለሥልጣን የፈቀደውን መጠን ነው፡፡ ቡኮው አብቅቶ ሊጡ ሊጋገር ሲል የተፈቀደው ኬሚካል መጠን ይጨመራል፡፡ ከዚያ በኋላ ያደረግነው ነገር ኬሚካል የተጨመረበትን እንጀራና ኬሚካል ሳይጨመርበት የተጋገረውን ማወዳደር ነው፡፡ ኬሚካል ያልተጨመረበት እንጀራ እንደተለመደው ሳይሻግት ሦስት ቀን ሲቆይ፣ ኬሚካል የተጨመረበት ግን ሳይሻግትና ለምለም እንደሆነ 10 ቀናት ቆይቷል፡፡ በቡኮው ሂደት ወቅት ኬሚካሉ ቢጨመር እህሉ እንዲቦካ የሚያደርጉትን ጥቃቅን ኦርጋኒዚሞች ይገድላቸዋል፡፡ ስለዚህ እንጀራን እንጀራ የሚያደርጉት ነገሮች አይኖሩትም ማለት ነው፡፡

በአገራችን የሚደረጉ የምርምር ውጤቶች ብዙውን ጊዜ ተግባራዊ ሆነው የኅብረተሰቡን ሕይወት ሲለውጡ አይታይምና የእናንተ የጥናት ውጤት ይህ ዕድል እንዳይገጥመው ምን እየሠራችሁ ነው?

የእንጀራ ፋብሪካ ከፍተው ወደ ውጭ የሚልኩ እንደማማ እንጀራ ያሉ ድርጅቶችን ለማነጋገር ሞክረናል፡፡ ነገር ግን ጥሩ ምላሽ አላገኘንም፡፡ ብዙ ጊዜ ዩኒቨርሲቲዎች የሚያደርጉት ምርምሮች ወደ ኅብረተሰቡ አይወርዱም፤ መደርደሪያ ላይ ነው የሚቀሩት፡፡ ምርምሮቹን ተቀብለው ሥራ ላይ የሚያውሏቸው ድርጅቶች የሉም፡፡ በአንፃሩ ግን በውጭ አገራት ምርምሮች የሚካሄዱት ኩባንያዎች ገንዘብ መድበው ስለሆነ፣ የጥናቱ ውጤት ይፋ ሲደረግ በባለቤትነት ይረከቡታል፡፡ በአገራችን ሳይንቲስቶችንና ባለሃብቶችን ለማገናኘት ጥረት ይደረጋል፡፡ ነገር ግን ይህን ነው የሚባል የተገኘ ውጤት የለም፡፡

የጥናታችሁን ውጤት ኅብረተሰቡ እንዲያውቀው የማስተዋወቅ ሥራ ሠርታችኋል?

ብዙ አልሄድንበትም እንጂ በተለያዩ መንገዶች ለማስተዋወቅ ሞክረን ነበር፡፡ ችግሩ ምን መሰለህ? ሰው ኬሚካል ሲባል ይፈራል፡፡ የኬሚካል ውህድ ያልሆነ ነገር የለም፡፡ ውሃም የሃይድሮጅንና የኦክሲጅን (H2O) ውሁድ ነው፡፡ በሰው ዘንድ “ኬሚካል መጥፎ ነው” የሚለው ግንዛቤ እንደ አንድ ችግር ሊወሰድ ይችላል፡፡ ሌላው ችግር ደግሞ ኬሚካሎችን ከውጭ አስመጥቶ እናቶች በየቤታቸው እንዲጠቀሙበት ማድረግም ቀላል አይደለም፡፡

በዚህ ዓይነት የእናንተም ጥናት የመደርደሪያ ጌጥ ከመሆን አልዳነም ማለት ነው?

እንደዚያ እንዳይሆን ፊታችንን ወደ ሌላ ዘዴ እያዞርን ነው፡፡ ሰው “ኬሚካል” የሚለውን ቃል ስለፈራ ፋብሪካ የሚመረቱትትን ሰው ሰራሽ ኬሚካሎች ትተን፤ ቡኮው ራሱ በተፈጥሯዊ ሂደት እንጀራ እንዳይሻግት የሚያደርጉትን ኬሚካሎች እንዲፈጥር ለማድረግ እየሠራን ነው፡፡ እስካሁን በእንጀራ ላይ የተሠራ ነገር ስለሌለ፣የሰው ፍራቻ ራሱ መነሻ ሐሳብ ሆኖን እየሠራንባት ነው፤ ውጤትም እያገኘንበት ነው፡፡ እንጀራ ቶሎ እንዳይሻግት ማድረግ ሌላም ጥቅም አለው፡፡ በምግብ ሰብል ራስን መቻል (ፉድ ሴኩሪት) ሲባል በምርት በመጨመር ብቻ የሚፈታ አይደለም - ያለውንም ይዞ በመቆየት ነው፡፡ በየቤቱ እየሻገተና እየደረቀ የሚደፋውን እንጀራ ብናሰላው ውጤቱ እጅግ አሳሳቢ ነው፡፡ ይኼ በእንጀራ ላይ ብቻ ያለ ችግር አይደለም፡፡ ሁሉም ነገር ሳይበላሽ የሚቆይበት ጊዜ ስለሌለ ብዙ ነገር ይበላሻል - ይባክናል፡፡ አሁን እኛ ጥናት ያደረግንነው የማንኛውንም ነገር የብልሽት ጊዜውን በማራዘም መጠቀም ይቻላል የሚል ነው፡፡ እንጀራ የምግብ ይዘቱ ዝቅተኛ ነው፡፡ ከአይረን (የብረት ማዕድን) በስተቀር ምንም የለውም የሚሉ ሰዎች አሉ፡፡

ይኼ ምን ያህል እዉነት ነው?

እኔ ለዚህ ሐሳብ ያለኝ ምላሽ ከተባለው በተቃራኒ ነው፡፡ እኔ እንዲያውም ለጤፍና ለእንጀራ መወደድ ምክንያቱ እንጀራ ስላለው ጥቅም በውጪው አገራት የሚሠሩት ከፍተኛ ጥናቶች ናቸው የሚል ሐሳብ አለኝ፡፡ ከተገኙ ውጤቶች አንዱ እንጀራ ግሉትን የለውም፡፡ ከግሉትን ነፃ ነው፡፡ ግሉትን ዳቦ ውስጥ የሚገኝ ፕሮቲን ሲሆን ዳቦው ኩፍ እንዳለ ይዞት የሚቆይ ነው፡፡ በእኛ አገር ውስጥ የለም እንጂ በአውሮፓና አሜሪካ ብዙ ሰዎች ለግሉትን ኬሚካል አለርጂ ናቸው - ግሉትን ኢንቶለራንት ይባላሉ። ስለዚህ እነዚህ ሰዎች ዳቦ ከበሉ ሆዳቸውን ያማቸዋል፣ ብዙ ችግሮችም ይደርስባቸዋል፡፡ አሁን በውጭ አገር የተደረጉ ጥናቶች የሚያመለክቱትና ኦንላይን የሚሸጠው እንጀራ ግሉትን የለውም፡፡ ዳቦ ውስጥ የሚገኘው ግሉትን ጤፍ ውስጥ የለም፡፡ ስለዚህ ግሉትን አልባነቱ እንጀራን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳጅ አድርጐታል።

ከዚህም በተጨማሪ በሌሎች የእህል ዘሮች ውስጥ የማይገኝ ጤፍ ውስጥ ብቻ የሚገኝ ላይሰን የሚባል አሚኖ አሲድ አለ፤ ጤፍ ከሌሎች እህሎች ጋር ሲነፃፀር እንደተባለው በካልሲየምና አይረንም የበለፀገ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ ደግሞ ፋይበር (አሰር) አለው፡፡ እንጀራ በልተህ ጥግብ ትላለህ፡፡ ሌላ ተጨማሪ ምግብ ሳትፈልግ ሰውነትህን መቆጣጠር ትችላለህ፡፡ አሜሪካኖችና አውሮፓውያን ብዙ ተጨማሪ ምግብ እየበሉ ከመጠን በላይ እየወፈሩ ነው፡፡ ስለዚህ ፋይበር ያለውን እንጀራ ሲበሉ ስለሚጠግቡ ተጨማሪ ምግብ አይፈልጉም፡፡ እንጀራ የደም ማጣራትም ተግባር አለው፡፡ ደም ካልተጣራ ለፊንጢጣና ለተለያዩ ካንሰሮች ያጋልጣል፡፡ የእንጀራ ፋይበር ጥቅም ከካንሰር ይታደጋል፡፡ ውጭ አገር ባሉ የኢትዮጵያውያን ሬስቶራንቶች ኢትዮጵያውያን ብቻ አይደሉም የሚመገቡት፡፡ በርካታ የውጭ አገር ዜጐችም ሲመገቡ ይታያሉ፡፡

እንጀራ ሳይቦካ ነው መጋገር ያለበት የሚል ነገር አለ፡፡

መቡካትና አፍለኛ መሆኑ ልዩነት አለው?

በቅርቡ አሜሪካ ፔንስቴት ዩኒቨርሲቲ ነበርኩ። እዚያ ትልቅ የእንጀራ ፕሮጀክት እየተሠራ ነው። እኔም የዚያ ፕሮጀክት አባል ነኝ፡፡ ኑትራ አፍሪካ ፉድ ፕሮሰሲንግ የሚባል ኩባንያ በደብረዘይት ተቋቁሟል፡፡ የኩባንያው ዓላማ እንጀራ አምርቶ ለውጭ ገበያ ማቅረብ ነው፡፡ እዚህ የሚበላው ዓይነት እንጀራ አሜሪካ መድረስ አለበት፡፡ እንዲህ ለማድረግ የእንጀራ የቡኮ ሂደት በጣም ከባድ ነው። እንዲቦካ የሚያደርገው ማይክሮ ኦርጋኒዝም ከአካባቢ ሁኔታ አንፃር ይለዋወጣል፡፡ ስለዚህ እዚህ የምናገኘውን የቡኮ ዓይነት እዚያ አናገኝም፡፡ በአገራችን የዳቦ እርሾ አለ፡፡ እርሾ ማለት ማይክሮ ኦርጋኒዝሞቹ ደርቀውና ታሽገው ማለት ነው፡፡ በእኛ አገር ግን እንዲህ ዓይነት ባህል ወይም የእንጀራ እርሾ የለም፡፡ ዱቄቱ የሚቦካው ቀደም ሲል እንጀራ ሲጋገር መጨረሻ ላይ ትንሽ ሊጥ በማስቀረት ነው፡፡

አዲስ እንጀራ ጋጋሪ ከጐረቤት እርሾ ተበድራ ነው የምታቦካው፡፡ በመሆኑም ቡኮውና እንጀራው እንደ ሴቷ ባልትና ከቤትቤት ይለያያል፡፡ ስለዚህ እንጀራን በፋብሪካ ደረጃ ለመጋገር ይህን ነገር መቀየር ያስፈልጋል፡፡ እንጀራ የራሱ እርሾ ያስፈልገዋል፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ የእርሾ ማይክሮ ኦርጋኒዝም እነማን ናቸው ብሎ ለይቶ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ እነሱን ከለየን፣ አሳድገን የእንጀራ እርሾ ማዘጋጀት እንችላለን፡፡ እንጀራ እርሾ ካለው እዚህና እዚያ የሚጋገረው እንጀራ ተመሳሳይ ይሆናል፡፡ ስለዚህ ይህ ኩባንያ እንጀራን ለውጭ ገበያ ለማቅረብ በሳይንሳዊ መንገድ ስለ እርሾ ይዘት ለይቶ ማወቅ አለበት፡፡ እንጀራ በአሜሪካ በሚፈለገው ሁኔታ እየተጋገረ አይደለም፡፡ ኒውዮርክ ሄጄ ነበር፡፡ እዚያ እንጀራ ለመጋገር አምቦ ውሃ ይጨምሩበታል።

ለምን?

አምቦ ውሃ ማለት ካንቦርዳይ ኦክሳይድ ማለት ነው፡፡ ሊጡ ውስጥ ካርቦንዳይ ኦክሳይድ ይጨምሩበታል፡፡ ካርቦንዳይ ኦክሳይዱ እሳት ሲያገኘው ትሽሽሽ! እያለ እየተንጣጣ ይወጣል። ሊጡ ሲኩረፈረፍ ይታያል፡፡ ጋገሪዋ/ው ምጣድ ላይ ሲያዞር ካርቦንዳይኦክሳይዱ ቷቷ! እያለ ይወጣና ዓይን ይፈጥራል፡፡ ዓይን ባያወጣስ? ከእንጀራ ኳሊቲ አንዱ ዓይኑ ነው፡፡ እንጀራ የሚወጣበትን ወጥ መያዝና ማርጠብ አለበት። ድፍን ካለ ወይም ዓይን ከሌለው ወጥ ስለማይዝ ለመብላት አመቺ አይደለም፡፡ ስለዚህ ዓይን እንዲያወጣ የራሳቸውን ዘዴ እየተጠቀሙ ነው፡፡ እኛ ጥሩ እንጀራ የሚባለው በስኩዌር ሳንቲሜትር ስንት ዓይን ያለው ነው የሚለው ደረጃ ላይ ደርሰናል። የእንጀራው ምስል በሚያጐላ መነፅር እየታየ ዓይኑ ይቆጠርና ትክክለኛ እንጀራ የሚባለው በሜትር ስኩዌር ከዚህ እስከዚህ ዓይን ያለው ነው ይባላል፡፡ በእኛ አገር ግን ምንም የሚታወቅ ነገር የለም፡፡

ጥሩ የሚባለው እንጀራም ውፍረትና ክብደቱም በመጠን መወሰን አለበት፡፡

እንጀራ ሌላ ኳሊቲ አለው?

የእንጀራ ሌላው ኳሊቲ መኮምጠጡ ነው። መኮምጠጡ ለምን ተፈለገ የሚለው ሳይንሳዊ መሠረት አለው፡፡ እኛ እንጀራን የምንበላው በወጥ ነው፡፡ የኮመጠጠ እንጀራ በወጥ ሲበላ ይጣፍጣል። የወጡን ጣዕም እየቀመስን ያለው በኮመጠጠ እንጀራ ላይ ነው፡፡ አፍለኛ እንጀራ የሚበላ ሰው “አልጣፈጠኝም ስኳር ስኳር አለኝ” የሚለው ለዚህ ነው፡፡ እንዲጣፍጥ የሚያደርገው አሲድ ጠፍቷል ማለት ነው፡፡ መኮምጠጡ ዋነኛው የእንጀራ ኳሊቲ ነው፡፡ የሚኮመጥጠው ደግሞ በተለያዩ አሲዶች አማካይነት ነው፡፡ ከሚቦካ ነገር፣ ከሊጥም ሆነ አይብ የተለያየ የመኮምጠጥ ኳሊቲ ነው የምናገኘው፡፡ ይህ ደግሞ የእኛ ሥራ ሳይሆን እንዳለ የማይክሮ ኦርጋኒዝሞቹ ነው፡፡ የወጣቱ ምሁር የምርምር ውጤት መደርደሪያ ላይ አልቀረም፡፡

መኖሪያቸውን በውጭ ያደረጉት አቶ ሲሳይ ሽመልስና ባልደረቦቻቸው በ50 ሚሊዮን ብር በቢሾፍቱ (ደብረ ዘይት) ከተማ ዘመናዊ የእንጀራ ማምረቻ ፋብሪካ ማቋቋማቸው ታውቋል። አቶ አሻግሬም የዚሁ ድርጅት አባል ነው፡፡ ፋብሪካው በሰዓት 50ሺህ፣ በቀን አንድ ሚሊዮን እንጀራ እንደሚያመርት ተጠቁሟል፡፡ በእንጀራ ጋገራ የተሰማሩ 300 ያህል ሴቶች ሥልጠና ከተሰጣቸው በኋላ የፋብሪካው የሽያጭ ወኪሎች እንደሚሆኑ አቶ ሲሳይ ተናግረዋል፡፡ የኑትራ አፍሪካን ምጣድ ዲዛይን የሠራው ሚካኤል ማ ይባላል፡፡ ማ በምዕራቡ ዓለም “ኢንቴል” የሚል አርማ የያዙ የተለያዩ የኮምፒውተር ዕቃዎችን ዲዛይን በመሥራት ይታወቃል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፡፡ እንደ ቢል ጌትስ ያሉ የዓለማችን ቱጃሮች የሚያሽከረክሯቸውን ውድ መኪኖች ዲዛይን ከሌሎች ጋር በመተባበር የሠራ ድንቅ የፈጠራ ባለቤት ነው፡፡ በቅርቡ የመርሰዲስ ኩባንያ ያመረታት ድንቅ መኪናም ማ ሚካኤል የፈጠራት መሆኑ ተገልጿል፡፡

  • በሰብ ሰሃራ አፍሪካ በጥንዶች መካከል በአማካኝ እስከ 15ኀ በመቶ የሚሆኑት የኤችአይቪ ውጤታቸው የተለያየ ሆኖ ይገኛል፡፡
  • በብዙ ጥናቶች እንደሚታየው ሴቶች 60 ወንዶቹ 40 ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ሆነው ይገኛሉ፡፡
  • ሳይንቲስቶችንም ግራ በሚያጋባ ሁኔታ ጥንዶች ውጤታቸው አንዳቸው ፖዘቲቭ አንዳቸው ደግሞ ኔጌቲቭ ይሆናሉ፡፡

በዚህ እትም ለንባብ የበቃው የአንድ ተሳታፊን ጥያቄ መሰረት ያደረገ ጉዳይ ነው፡፡ ለጥያቄው ማብራሪያ እንዲሰጡ የጋበዝናቸው ዶ/ር እያሱ መስፍን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ፋክልቲ መምህር እና የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ናቸው፡፡ ቀጥሎ የምታነቡት ተሳታፊዋ የላኩትን ጥያቄ ነው፡፡ ውድ ኢሶጎች... .....እኔ ኤች አይ ቪ ፖዘቲቭ ስሆን ባለቤ ግን ኔጌቲቭ ነው፡፡እኔ እስከአሁን ድረሰ ምንም የኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ አይደለሁም ፡፡ የግብረስጋ ግንኙነት የምንፈጽመውም በኮንዶም ነው፡፡ ነገር ግን ልጅ ለመውለድ በጣም ስላማረኝ አንድ ነገር አሰብኩ፡፡ ይኼውም ከግንኙነት በሁዋላ በኮንዶም ውስጥ ያለውን የዘር ፈሳሽ ባለቤ ወደእኔ ማህጸን ውስጥ እንዲያፈሰው እና ማርገዝ እንድችል ነው፡፡

ነገር ግን የፈለግነውን ነገር ከማከናወናችን በፊት መጠየቅ የምፈልገው... በጠቆምኩት መንገድ ሙከራ ብናደርግ ልጅ ማርገዝ እችላለሁ? ልጅ ማርገዝ ብችልስ ምን ያህል ጤናማ ይሆናል? ልጅ ከአረገዝኩ በሁዋላ የፀረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ መሆን ይጠበቅብኛል? ለእነዚህ ጥያቄዎች እና ተያያዥ ለሆኑት ሁሉ መልስ እንደማገኝ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ .. ዶ/ር እያሱ መስፍን ከአሁን ቀደም ለዚሁ እትም የባለትዳሮችን በኤችአይቪ ቫይረስ ውጤት መለያየት በሚመለከት መልስ ሰጥተዋል፡፡ .....ከጥንዶች ወይም ከባለትዳሮች መካከል አንዳቸው ፖዘቲቭ ሌላኛው ደግሞ ኔጌቲቭ በመሆን የኤችአይቪ ውጤት መለያየት ሲኖር በእንግሊዝኛው ዲስኮርዳንስ ይባላል፡፡ይህ በአሁኑ ጊዜ በጥንዶች መካከል ቁጥሩ እየጨመረ የመጣ ነው፡፡

በተለይም በሰብ ሰሃራ አፍሪካ በጥንዶች መካከል በአማካኝ እስከ 15ኀ በመቶ የሚሆኑት የኤችአይቪ ውጤታ ቸው የተለያየ ሆኖ ይገኛል፡፡ ጥንዶች በጋር እየኖሩ የተለያየ ውጤት የሚኖርበት ምክን ያት የተለያየ ነው፡፡አንዱ በቅርብ ጊዜ የተጋቡ ከሆኑ ወይንም አንዱ ፖዘቲቭ ሆኖ ገና ወደሌላው እስኪተላለፍ በሚወስደው ጊዜ ምክንያት ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ለረጅም ጊዜ በትዳር አብረው እየኖሩም አንዱ ፖዘቲቭ ሌላው ደግሞ ኔጌቲቭ የመሆን ነገር ይታያል፡፡ በኤችአይቪ የመያዝ ሁኔታ ከሰው ሰውም ይለያያል፡፡ አንዳንዶች በቫይ ረሱ ያለመያዝ ሁኔታ ሲታይባቸው ሌሎች ደግሞ ቶሎ የመያዝ ሁኔታ ይኖራቸዋል፡፡ እንደገናም በደም ውስጥ ያለው የቫይረስ መጠንም ቁጥሩ ከፍ ያለ ከሆነ ወይንም ብዙ ቆይቶ ብዙ የተጎዳ ከሆነ ለመተላለፍ ከፍ ያለ እድል ይኖረዋል፡፡

የኤችአይቪ መድሀኒት ሙሉ በሙሉ በትክክል የሚወስዱ ሆነው ነገር ግን ሳይከላከሉ ወይንም በኮንዶም ሳይ ጠቀሙ የወሲብ ግንኙነት የሚያደርጉ ከሆነ አሁንም ቫይረሱ የመተላለፍ እድል ይኖረ ዋል፡፡ ነገር ግን በተለያዩና በማይታወቁ ምክንያቶች ለሳይንቲስቶችም ግራ በሚያጋባ ሁኔታ ጥንዶች አንዳቸው ፖዘቲቭ አንዳቸው ደግሞ ኔጌቲቭ ሆነው አብረው ይኖራሉ፡፡ አብረው በሚኖሩ ጥንዶች በአማካኝ ከአንድ መቶ እስከ ሁለት መቶ ግንኙነት ውስጥ በአንዱ ኤችአይቪ ቫይረስ እንደሚተላለፍ ይገመታል፡፡ ስለዚህም ጥንዶች ምንም ኮንዶም የማይጠቀሙ ከሆነ በአመቱ መጨረሻ ከመቶው አስሩ በቫይረሱ ሊያዙ ይችላሉ፡፡ ይህን ንም ለመከላከል በማንኛውም ጊዜ በወሲብ ግንኙነቱ ወቅት ኮንዶም እንዲጠቀሙ ግድ ነው፡፡..... ኢሶግ፡ የዘር ፈሳሽን ከኮንዶም ወደማህጸን በማስገባት ማርገዝ ይቻላልን? ዶ/ር ኢያሱ፡ ይህ ጥያቄ የብዙዎች ከኤችአይቪ ጋር የሚኖሩ ሰዎች ጥያቄ ነው፡፡

የወንድ የዘር ፍሬ መቅስቈቂ ሰስቁቁ በተፈጥሮው ጭራ ያለው መዋኘት ወይንም መንቀሳቀስ የሚችል ነው፡፡ ስለዚህም ምቹ ሁኔታ ከተፈጠረለት ካለበት ስፍር ዋኝቶ በመንቀሳቀስ እርግዝና እንዲፈጠር ያስችላል፡፡ ለምሳሌ ሙሉ በሙሉ ወሲባዊ ግንኙነት ሳይፈጸም ወይንም ክብረንጽህና ሳይገሰስ በብልት አካባቢ የዘር ፈሳሹ በመፍሰሱ ብቻ እርግዝና የሚከሰትበት አጋጣሚ አለ፡፡ ስለዚህ በኮንዶም ውስጥ የፈሰሰ የዘር ፈሳሽ ወደማህጸን የሚገባበት አጋጣሚ ከተፈጠረ ማርገዝ ይቻላል፡፡ ነገር ግን ወደ ጠያቂዋ ሁኔታ ስንመለስ ወሲባዊ ግንኙነት የምትፈጽመው በኮንዶም ሲሆን ኮንዶም የተዘጋጀው ደግሞ ባብዛኛው እርግዝ ናን ለመከላከል ሲሆን በሚሰራበት ጊዜ በወንድና በሴት ዘር መካከል እንዳይገናኙ እንደግድግዳ ከመከላከል በተጨማሪ የሚጨመርበት የኬሜካል ውሁድ አለ፡፡ እነዚህ ኬሚካሎች የወንዱን የዘር ፍሬ መዋኘት እንዳይችል ወይንም እንዳይንቀሳቀስ በማድረግ አቅሙን የማዳከም ስራ ይሰራሉ፡፡

ስለዚህ በዚህ መልክ የተጠራቀመው የዘር ፈሳሽ ውጤታማ ላይሆን ይችላል፡፡ በእርግጥ ማርገዝ ከተቻለ በሚረገዘው ልጅ ጤና ላይ ምንም የሚያስከትለው ጉዳት ወይንም የጤና ችግር የለም፡፡ ኢሶግ፡ የወንድም ይሁን የሴት የዘር ፍሬ ከፈሰሰ በሁዋላ ምን ያህል የቆይታ እድሜ ይኖረዋል? ዶ/ር ኢያሱ፡ የወንድና የሴት የዘር ፍሬዎች ቆይታ ይለያያል፡፡ ከግንኙነት በሁዋላ የወንዱ የዘር ፈሳሽ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ በመዋኘት ከማህጸን በር አልፎ ከማህጸን ቱቦ ይደርሳል፡፡ ሁኔታዎች ለመቆየት ከተመቻቹለትም እስከ 72/ሰአት ድረስ ቆይታ ያደርጋል፡፡ የሴቷ የዘር ፍሬ ግን ሁኔታዎች በተሙዋሉበት ከ24-48 ሰአት ድረስ ብቻ መቆየት ይችላል፡፡ ኢሶግ፡ አንዲት ሴት በኮንዶም የተጠራቀመ የዘር ፈሳሽን ወደ ማህጸን በግልዋ ማስገባት ትችላለች? ዶ/ር ኢያሱ፡ የዘር ፈሳሽን ወደማህጸን ማስገባት የሚል አሰራር በግለሰብ ደረጃ የለም፡፡ ምናልባትም ሰዎች የተፈጥሮን አቀማመጥ ካለመረዳት የሚያስቡት ሊሆን ይችላል፡፡

በመጀመሪያ ብልት አለ፡፡ ከዚያም የማህጸን በር ይገኛል፡፡ ከዚያ በሁዋላ የማህጸን ቱቦ ጋ ደርሶ ፈሰሽን ማስገባት ሲቻል ነው እርግዝና ይኖራል የሚባለው፡፡ ብዙዎች የሚያስቡት ልክ ከብልት ቀጥሎ የሚያገኙትን አካል ማህጸንን እንደሚያገኙ አድርገው ከሆነ ስህተት ነው፡፡ ከማህጸን ቱቦ መድረስ የሚቻለው ክኒካል በሆነ የህክምና አሰራር እንጂ በግል አይደለም፡፡ በእርግጥ የወንድ የዘር ፈሳሽ በብልት እና በማህጸን በር አካባቢ በመፍሰሱ ብቻ የመቆየት እድሉን ካገኘ እራሱ ዋኝቶ እርግዝና እንዲከሰት የሚያደርግበት አጋጣሚ ስለሚስተዋል ይህንን እድል መጠቀም ይቻል ይሆናል፡፡ ነገር ግን ሊታወቅ የሚገባው የምንጠቀምባቸው ኮንዶሞች ፀረ ስፐርም ያልሆኑና የማያዳክሙ አይነት መሆናቸውን ማረጋገጥ ነው፡፡ ኢሶግ፡ ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ወይንም የተለያየ ውጤት ያላቸው ሰዎች ልጅ ለመውለድ ምን ማድረግ አለባቸው? ዶ/ር ኢያሱ፡ ይህንን ፍላጎት ለማሟላት ብዙ መፍትሔዎች አሉ፡፡ ወሲባዊ ግንኙነት ከኮንዶም ውጪ ከተደረገ ከአንዱ ሰው ወደሌላው እንዲሁም ወደሚረገዘው ልጅ ቫይረሱ መተላለፉ እርግጥ ነው፡፡

ነገር ግን ይህንን የመተላለፍ እድል ለመቀነስ መደረግ የሚገባቸው ጥንቃቄዎች አሉ፡፡ የመጀመሪያው የቫይረሱ መጠን በሰውነትዋ ውስጥ አድጎ ከሆነ ወይንም የመከላከል አቅሙዋ ቀንሶ ከሆነ የፀረ ኤችአይቪ መድሀኒት በመውሰድ በደምዋ ውስጥ የሚገኘውን የቫይረስ መጠን እንዲቀንስ ማድረግ ነው፡፡ በዚህም አንዳቸው ለሌላኛው የሚያስተላልፉትን ቫይረስ ከመቀነስ ባሻገር ጤነኛ ልጅ ለመውለድ ያስችላቸዋል፡፡ በእርግጥም ቫይረሱ የመተላለፉን አደጋ ሙሉ በሙሉ ያስወግዳል ባይባልም እጅግ ይቀንሰዋል፡፡ ስለዚህ ወደሕክምናው በመሄድ አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ ይጠቅማል፡፡ የፀረ ኤችአይቪ መድሀኒቱን ወስዶ በደም ውስጥ ያለውን ቫይረስ መቀነሱ ከታወቀ በሁ ዋላ የወር አበባ ቀንን በመቁጠር ማርገዝ በሚቻልባቸው ቀናት ብቻ ያለኮንዶም ግንኙነት ማድረግ እንደ አንድ አማራጭ ሊያዝ ይችላል፡፡ ይህ ግን ውስን ለሆነ ቀን እንደመጨረሻ አማራጭ የሚወሰድ መሆኑ ልብ ሊባል ይገባል፡፡

በእኛ አገር ባይኖርም ባደጉ አገሮች እንደ አማራጭ ከሚወሰዱ መንገዶች መካከል የወንድ የዘር ፍሬ ተወስዶ በማሽን የሚታጠብበት ነው፡፡ የወንዱ የዘር ፍሬ ከቫይረሱ ከጸዳ በሁዋላ በመርፌ ወደ ሴቷ ማህጸን እንዲገባ በማድረግ ልጅ መውለድ የሚቻልበት መንገድ አለ፡፡ በአጠቃላይ ግን ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩም ሆኑ ማንኛውም ሰው እርግዝናን ሲያስብ አስቀድሞ ሐኪምን ማማከር እንደሚገባ መዘንጋት የለበትም፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

በ2012 -13 የውድድር ዘመን የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች ዛሬ እና ነገ ሙሉ ለሙሉ ሲጠናቀቁ በየሊጐቹ የሻምፒዮናነት ፉክክሩ ብዙም አጓጊ ያልነበረ ቢሆንም የታየው የገቢ መነቃቃት የአውሮፓ እግር ኳስ ትርፋማነትን አሳይቷል፡፡በስፖንሰርሺፕ እና በተለያዩ የንግድ እንቅስቃሴዎች የሚገኙ ገቢዎች መሟሟቅ የተጨዋቾች የደሞዝ ክፍያ እና የዝውውር ገበያውን ሂሳብ እያሳደገ ነው፡፡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ማን ዩናይትድ በውድድሩ የተሳትፎ ታሪኩ 20ኛውን ፤ በስፔን ፕሪሚዬራ ሊጋ ባርሴሎና በውድድሩ የተሳትፎ ታሪኩ 22ኛውን፤ በጀርመን ቦንደስ ሊጋ ባየር ሙኒክ በውድድሩ የተሳትፎ ታሪኩ 23ኛውን፤ በጣሊያን ሴሪኤ ጁቬንትስ በውድድሩ የተሳትፎ ታሪኩ 29ኛውን እንዲሁም በፈረንሳይ ሊግ 1 ፓሪስ ሴንትዠርመን በውድድሩ የተሳትፎ ታሪኩ 3ኛውን የሻምፒዮናነት ክብራቸውን አግኝተዋል፡፡ አምስቱ የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች ዘንድሮ በተለይ በማልያ ስፖንሰርሺፕ ገቢ እና በቴሌቭዥን የስርጭት መብት የሚያገኙት ገቢያቸው ጨምሯል፡፡ በውድድር ዘመኑ ከማልያ ስፖንሰርሺፕ አምስቱ ምርጥ ሊጎች በድምሩ እስከ 315 ሚሊዮን ፓውንድ ሰብስበዋል፡፡

ከዚሁ ገቢ በሚወዳደሩበት 20 ክለቦች 11 የስፖርት ትጥቅ አምራች ኩባንያዎችን ያሰራው የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በ117.3 ሚሊዮን ፓውንድ ገቢ የአንበሳውን ድርሻ ወስዷል፡፡ በቴሌቭዥ ንስርጭት መብት ደግሞ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ለቀጣዮቹ 3 የውድድር ዘመናት 6 ቢሊዮን ፓውንድ ለማግኘት ውሉን ሲያድስ የጀርመኑ ቦንደስ ሊጋም በተመሳሳይ ወቅት 2.5 ቢሊዮን ፓውንድ በላይ ለመሰብሰብ እንደተዋዋለ ታውቋል፡፡

በአንድ የውድድር ዘመን በሚያስገኘው የገቢ መጠን ከአውሮፓ አምስት ታላላቅ ሊጎች የሚመራው የእንግሊዙ ፕሪሚዬር ሊግ ከ2.11 ቢሊዮን ፓውንድ በላይ በመሰብሰብ ነው፡፡ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ ደግሞ በየዓመቱ 1.40 ቢለዮን ፓውንድ ገቢ እየሰራ ሁለተኛ ደረጃ አለው፡፡ የስፔኑ ላሊጋ 1.37 ቢሊዮን ፓውንድ፤ የጣሊያኑ ሴሪኤ 1.29 ቢሊዮን ፓውንድ እንዲሁም የፈረንሳዩ ሊግ 1 በ900 ሚሊዮን ፓውንድ ዓመታዊ ገቢ በማስመዝገብ ተከታታይ ደረጃ አላቸው፡፡

በውድድር ዘመኑ በስታድዬም ተመልካች ብዛት ግንባር ቀደሙ የጀርመን ቦንደስሊጋ ሲሆን የሊጉ አንድ ጨዋታ በአማካይ የሚያገኘው የተመልካች ብዛት 42429 ነው፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ 35903 ፤ የስፔን ላሊጋን 29353፤ የጣሊያን ሴሪኤ 24752 እንዲሁም የፈረንሳይ ሊግ1 19168 ተመልካችን ብእያንዳንዱ ጨዋታ በአማካይ ያገኛሉ፡፡ የእንግሊዙ ፕሪሚዬር ሊጉ ነገ ሲገባደድ በተመሳሳይ ሰዓት የሚደረጉ ሁለት ወሳኝ ጨዋታዎች ይጠበቃሉ፡፡

ጨዋታዎቹ በ3ኛ ደረጃ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የምድብ ማጣርያን ተሳትፎ ለማግኘት በአንድ ነጥብ ተበላልጠው ሶስተኛ እና አራተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙትን አርሰናልና ቶትንሃም የሚያተናንቁ ናቸው፡፡ ቶትንሃም ከሊጉ ላለመውረድ የሚጫወተውን ሰንደርላንድ ሲገጥም ኒውካስትል ዩናይትድ ከአርሰናል ይገናኛል፡፡ በጣሊያን ሴሪኤ ሲዬና ከሚላን በሚያደርጉት ጨዋታም የሻምፒዮንስ ሊግ እጣ ይወሰናል፡፡ ኤሲ ሚላን በባላቶሊ እየተመራ በሴሪኤው ሶስተኛ ደረጃ ይዞ ለመጨረስ ከባድ ፈተና ይገጥመዋል፡፡ በስፔን ላሊጋ በ እስከ አራት ባለው የሊጉ ደረጃ ለመጨረስ ሁለት ፍልሚያዎች ይጠበቃሉ፡፡በእነዚህ ጨዋታዎች ጌታፌ ከቫሌንሽያ እንዲሁም ሲቪያ ከሪያል ሶሲየዳድ ይገናኛሉ፡፡ በጀርመን ቦንደስ ሊጋ ፍራይበርግ ከሻልካ 4 ዛሬ ይጫወታሉ፡፡

“እናቴ፤ ምነው በእንቁላሉ ጊዜ በቀጣሽኝ!”

        እናንተዬ፤ የሰሞኑን የሙስና ዘመቻ እንዴት አያችሁት? (የሙስና አብዮት ማለቴ ነው!) ባለፈው ሳምንት በፓርላማ የመ/ቤታቸውን ሪፖርት ያቀረቡት የፌደራል የፀረሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር አሊ ሱሌማን፤ የፀረ- ሙስና እርምጃው በግርግርና በዘመቻ የሚካሄድ እንዳልሆነ ነግረውናል (እኛስ መች ግርግር ፈለግን) እንዲያም ሆኖ ግን ሁሉነገሯን በዘመቻ የምትመራ ለምትመስለው ጦቢያችን የኮሚሽነሩ አባባል ትልቅ ለውጥ ነው፡፡ ሥርነቀል አብዮት! ባለፈው ጊዜም ጠ/ሚኒስትሩ--“ይሄ በዘመቻ የሚሰራ ነገር አይደለም” ሲሉ ሰምቼአለሁ (ምኑን ይሆን ግን?) በነገራችሁ ላይ በፓርላማ የሳቅ ድርቀት መግባቱን ያወቅሁት ኮሚሽነሩ “ኮሽ አለ ተብሎ ተኩስ አይከፈትም” ብለው ከመናገራቸው ቤቱ በሳቅ ሲሞላ ነው፡፡

በፓርላማ ብቸኛውና ታሪካዊው የተቃዋሚ ተወካይ አቶ ግርማ ሰይፉም፤ ተጠርጥረው የተያዙትን የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ሃላፊዎችና ባለሃብቶች በተመለከተ በሰጡት አስተያየት “ግንድ ባይሆኑም ከቅርንጫፍ ትንሽ ከፍ ከሚሉት መጀመሩ ያስመሰግናል” ሲሉ አፈጉባኤው በሳቅ ፈርሰው እኔንም ፍርስ አደረጉኝ (ሳቅ እንደ ጉንፋን ይጋባል እንዴ?) ይሄም ራሱ ፓርላማው የሳቅ ድርቅ እንዳጠቃው ሁነኛ ማስረጃ ይመስለኛል (ግን በስንቱ ነው የምንጠቃው ?) እኔ የምለው ---- በቃ እያሳቀ ቁምነገር የሚናገር ፖለቲከኛ የለንም ማለት ነው ? እንዴ ---- ሳቅማ የግድ ያስፈልጋል፡፡ እንደነኬንያ የፓርማ አባላት እስከ 100ሺ ብር ደሞዝ ቢከፈላቸው እንኳን የራሳቸው ጉዳይ እንላቸው ነበር፡፡

ደሞዝም ሳቅም መንፈግ ግን ከሰብዓዊ መብት ጥሰት ብዙም አይለይም (ህገመንግስቱ ላይ ባይካተትም) እውነቴን ነው---- ሳቅ እኮ ጤና ነው! ከፖለቲካ ጋር ሲሆን ደግሞ አሉታዊ ኬሚካሎችን ስለሚያስወግድ የበለጠ ጤና ይሆናል፡፡ እግረመንገዴን በኢቴቪም ሆነ በፓርላማ ሲናገሩ ኩስትርትር የሚሉብንን ባለሥልጣናት “ተዉ አትኮሳተሩብን” ልላቸው እፈልጋለሁ (እኛው መርጠናቸው ቁጣ አለብን እንዴ?) እኔ የምለው ግን የፀረ - ሙስና ኮሚሽን በሙስና የተጠረጠሩ ባለስልጣናትን ለመመርመር በፈለገ ቁጥር ጠ/ሚኒስትሩን ማስፈቀድ አለበት እንዴ? (ለጠቅላላ እውቀት ያህል ነው) ግን እኮ እሳቸው መሪ እንጂ መቼም ህግ አይደሉም፡፡ እናም አንዴ ተስማምቶ ህጉን ማርቀቅ ይሻላል እንጂ--- ሞሳኝ ባለሥልጣን በተገኘ ቁጥር ወደ ጠ/ሚኒስትሩ ቢሮ መሮጥ “ፌር” አይመስለኝም፡፡ (ያውም በዘንድሮ የትራፊክ መጨናነቅ) አረ እሳቸውንም ምቾት መንሳት ነው፡፡ እርግጠኛ ነኝ እንደእኔ ያለው ተራ ዜጋም ሆነ ባለከባድ ሚዛን ባለሥልጣኑ ሙስና ከፈፀመ በህግ ፊት እኩል ነው (ተሳሳትኩ እንዴ?) በአንድ አገር ሁለት ህግ አይወጣም ብዬ እኮ ነው፡፡

እንደኔ ሰሞኑን በሙስና ዙርያ የሚሰጡ አስተያየቶችን በቅጡ ተከታትላችሁ ከሆነ፤ ብዙዎች የመንግስትን እርምጃ በጥርጣሬ እንደተመለከቱት ትረዳላችሁ፡፡ “ኢህአዴግ ልማዱ ነው… በፖለቲካ የሚፈልጋቸውን ሰበብ እየፈጠረ ማጥመድ ይወዳል”፣ “መንግስት እነዚህን ባለሥልጣናት ሲይዝ ሌላ ዓላማ ከሌለው እርምጃው ይበል የሚያሰኝ ነው”፣ “እቺማ የፖለቲካ ጨዋታ ናት” ወዘተ -- ዓይነት አስተያየቶች ጥርጣሬንና እምነት ማጣትን የሚጠቁሙ ናቸው (እንዴት መታመን እንዳለበት ማሰብ የመንግስት የቤት ሥራ ነው!) በነገራችሁ ላይ ኢቴቪ በሙስና ተጠርጥረው በተያዙ ባለስልጣናት ዙሪያ የሚሰጡ አስተያየቶችን (ውዳሴም ትችትም) በሚዛናዊነት ማቅረቡ አስደምሞኛል (ለአንድ ሳምንት ቢሆንም አድናቂው ነበርኩ) ባለፈው ወር የተካሄደውን የአዲስ አበባና የአካባቢ ምርጫ በተመለከተ ኢራፓ የሰጠውን መግለጫ እንደወረደ ማቅረቡም አስገርሞኛል (ኢቴቪ ከኢህአዴግ እጅ ወጣ እንዴ?) ይታያችሁ ---- ፓርቲው የሰጠው መግለጫ እኮ ኢህአዴግና ቦርዱ ነፃና ፍትሃዊ ብለው በትብብር ያሞካሹትን ምርጫ “አፈር ድሜ” የሚያስበላ ነው፡፡ በጥቅሉ ምርጫው ነፃና ፍትሃዊ እንዳልሆነ፣ ዓለምአቀፍ የምርጫ መመዘኛዎችንም እንደማያሟላ ነው ፓርቲው የገለፀው፡፡

ኢቴቪም ያንኑ በቀጥታ አስተላለፈው፡፡ እኔ ግን ምን ደስ እንዳለኝ ታውቃላችሁ? ኢራፓ እንዳለው ምርጫው ነፃና ፍትሃዊ ባይሆን እንኳ ኢቴቪ ቅሬታውን ነፃና ፍትሃዊ በሆነ መንገድ መዘገቡ፣ ለእኔ ነፃ ምርጫ ከማካሄድ እኩል ነው፡፡ ምን አለፋችሁ --- ኢቴቪ ነፃ ወጣ ብዬ እልልልል-- ብያለሁ (ቀጣይነቱ ላይ ጥርጣሬ ቢኖረኝም!) ወደ ሰሞኑ የሙስና አብዮት እንመለስ፡፡ አንድ ስለሙስናው አብዮት በኢቴቪ አስተያየት የሰጠ ነጋዴ ምን ቢል ጥሩ ነው? “ጫፍ ጫፉ ነው የተነካው፤ ተሰርስሮ ከተገባ ብዙ ነገር አለ…” (ይሞታል እንዴ ታዲያ!) አብዛኞቹ አስተያየት ሰጪዎች በጋራ የሚስማሙበት ጉዳይ ምን መሰላችሁ? አንደኛ “ለሙስና እዚህ ደረጃ መድረስ ተጠያቂው ራሱ መንግስት ነው” የሚል ነው (መንግስት መልስ ይስጥበት) ሁለተኛው “በሞሳኞች ላይ የተወሰደው እርምጃ በጣም ዘግይቷል” የሚል ነው፡፡ (ለአንድ መ/ቤት 2 ዓመት ገደማ ምን አላት!) ኮሚሽነሩ እንዳሉት- ዘራፊዎቹ እንደሆኑ ከህዝብ አያመልጡም (ግን እኮ ስንቶቹ አምልጠዋል!) እኔ ደግሞ እንዲህ አሰብኩ፡፡

ራሳቸው ሙሰኞች በሆዳቸው መንግስትን እያማረሩ ቢሆንስ? “እናቴ፤ ምነው የእንቁላሉ ጊዜ በቀጣሽኝ!” እያሉ፡፡ (ለማንም ሳይሆን ለራሳቸው!) ቢሉም እኮ አይፈረድባቸውም። ብዙ ሚሊዮን ብሮችን (ያውም በጠፋ ገንዘብ!) ብዙ ሺ ዶላሮችን (ያውም በሌለ ዶላር!) ብዙ ሺ ፓውንዶችን፣ በርካታ የቦታ ካርታዎችን ከመሰብሰባቸዉ በፊት ማስጠንቀቂያ ወይም ማሳሰቢያ ቢጤ ቢሰጣቸው ኖሮ (የፓርቲ ግምገማ ቀረ መሰለኝ?) ለአሁኑ ባለ ከባድ ሚዛን የሙስና ወንጀል ተጠርጣሪነት ባልደረሱ ነበር (ተጠርጣሪ እንጂ ወንጀለኞች እንዳልሆኑ ልብ ይሏል!) ሰሞኑን እኔም ስለዚሁ የሙስና ጉዳይ ሳስብ ነው የሰነበትኩት (እንደባለሃብትና እንደባለሥልጣን ሳይሆን እንደዜጋ) እናም አንድ ሃሳብ ብልጭ አለልኝ፡፡ ይሄ የሙስና አብዮት በፈነዳበት በዚህ ታሪካዊ ወቅት ኢትዮጵያን የሚመሩት አፄ ምኒልክ ቢሆኑ ኖሮ (ቢሆኑ ነው ያልኩት!) ምን ያደርጉ ነበር?--- ብዬ ማሰብ ጀመርኩ - በታሪክ ባቡር ወደ ኋላ ተንሻትቼ፡፡

እናም ምኒልክ ከእቴጌ ጣይቱ ጋር ተማክረው የሚከተለውን ደብዳቤ ሊፅፉ እንደሚችሉ ገመትኩ፡፡ “የአገሬ ሹማምንት ሆይ፡- በእውቀትም ይሁን ያለ እውቀት እስከዛሬ በፈፀምከው በደል አልጠይቅህም፡፡ ይቅር ብዬሃለሁ። አንተም ታዲያ ትዕዛዜን ከልብህ ሰምተህ እንደ ቃሌ ፈፅም፡፡ ጉቦ ተቀብለህ በሻንጣህም ሆነ በፍራሽህ ስር ያኖርከው የአማሪካም ይሁን የአውሮጳ ወይም ደግሞ የእስያ ገንዘብ ካለ ራስህ ወስደህ ለመንግስት ግምጃ ቤት ቆጥረህ አስረክብ፡፡ ለራስህና ለቤተሰቦችህ ከሚበቃህ ውጭ የያዝከው መሬት ካለም ምንም ሳታመነታ ተመላሽ አድርግ፡፡ ያልኩህን በአስር ቀን ውስጥ ሳትፈፅም ቀርተህ፤ ወታደሮቼ ቤትህን በርብረው ካገኙብህ ግን እመቤቴን እልሃለሁ አልምርህም! ዳግማዊ አፄ ምኒሊክ ንጉሰ ነገስት ዘኢትዮጵያ!!” አያችሁ … አፄ ምኒልክ ይሄን የመሰለ የተማፅኖ ደብዳቤ (ማስጠንቀቂያም ሊባል ይችላል) የሚፅፉት የፀረ ሙስና ኮሚሽን ስለሌላቸው ይሆናል፡፡

ወይም ደግሞ ህዝቡ የምለውን በጄ ብሎ ይሰማኛል በሚልም ሊሆን ይችላል፡፡ የአሁኗ ኢትዮጵያ መሪ ደግሞ የትኛውን ብልሃት እንደሚጠቀሙ አብረን የምናየው ይሆናል (ዕድሜ ከጤና ለሳቸውም ለእኛም ይስጠን!) እንግዲህ አንዴ ገብተንበታልና በዚሁ የሙስና አጀንዳ እንቀጥል፡፡ እናም እስቲ ባህር ማዶ ተሻግረን አንዳንድ የሙስና ታሪኮችን እንቃኝ፡፡ (መማርያ ቢሆነን!) እ.ኤ.አ በ2008 ዓ.ም ሲመንስ የተባለ የጀርመን ኩባንያ የአርጀንቲና መንግስት ቱባ ቱባ ባለስልጣናትን በከፍተኛ ገንዘብ በመደለል የዜጐች መታወቂያ ካርድ ለመስራት የወጣውን ጨረታ ለማሸነፍ ይፈልጋል፡፡ በእርግጥ ገንዘቡ ቀላል አልነበረም፡፡ የቢሊዮን ዶላር ኮንትራት ነው፡፡ ስለዚህም ኩባንያው በደንብ አስቦና አስልቶ ገባበት፡፡ ለአርጀንቲና መንግስት ባለስልጣናትም 27 ሚ. ዶላር ጉቦ ከፈለ፡፡ የማታ ማታ ግን ጉቦ ሰጪዎቹ የኩባንያው ባለቤቶችም ሆኑ ተቀባዮቹ ባለስልጣናት ከተጠያቂነት አልዳኑም፡፡

በ2010 ዓ.ም ደግሞ BAE ሲስተምስ የተባለ የአሜሪካ ኩባንያ፤ ለሳኡዲ አረቢያ የብዙ ቢሊዮን ዶላሮች የጦር መሳሪያ ሽያጭ ለመፈፀም ሲል ለሳውዲ አምባሳደር 2ሚ.ዶላር ጉቦ እንደሰጠ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ (ይታያችሁ የ2ሚ. ዶላር ጉቦ?) የሙስና ወጋችንን እንቀጥል - ከአገር አገር እየተዟዟርን፡፡ ቼን ሹዩ-ቢያን የታይዋን ፖለቲከኛ ነበሩ (ፖለቲካ ካለ ቅሌት አለ እንዳትሉኝ!) ፖለቲከኛም ስላችሁ ቀላል ፖለቲከኛ እንዳይመስሏችሁ - ባለ ከባድ ሚዛን ነበሩ፡፡ ምንም እንኳን ከድሃ ቤተሰብ የተገኙ ቢሆኑም (ፖለቲከኛ ሁሉ ድሃ ነው እንዴ?) ከፍተኛው የሥልጣን እርከን ላይ መድረስ የቻሉ ሰው ነበሩ - ቼን፡፡

በፈረንጆቹ አቆጣጠር በ2000 ዓ.ም የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሆነው የተመረጡት ቼን፤ (ቻው ቻው ድህነት አሉ ማለት ነው?) ለሰፊው ህዝብ የቆሙ ተራማጅ መሪና አዝናኝ እንደነበሩ ይነገርላቸዋል፡፡ በ2004 ዓ.ም ለሁለተኛ ጊዜ በምርጫ አሸንፈው በፕሬዚዳንትነታቸው ቀጠሉ (የምርጫው ዲሞክራሲያዊነት አልተረጋገጠም!) የቼን ቅሌት አሃዱ ብሎ የጀመረው ከሁለት ዓመት በኋላ ነበር - በ2006 ዓ.ም፡፡ መጀመርያ የተነጀሱት የሴት ልጃቸዉ ባል በህገወጥ የንግድ ሥራ በተከሰሰ ጊዜ ነበር፡፡ በዚያው ዓመት ሚስታቸው በሙስናና በሃሰተኛ የገንዘብ ኖት ህትመት ክስ ተመሰረተባት። 21 ሚ. ዶላር በስዊዘርላንድ ባንክና በሌሎች ሁለት የውጭ አገር ባንኮች ማስቀመጧም ተረጋግጧል፡፡ ቼን ራሳቸውም ቢሆኑ ሥልጣናቸውን ያለ አግባብ ተጠቅመዋል የሚል ክስ ነበረባቸው፡፡ (ባልና ሚስት ከአንድ ወንዝ ይቀዳሉ እንዲሉ!) ሆኖም ያለ መከሰስ መብታቸው ፍ/ቤት ከመቆም አተረፋቸው (አይ ሥልጣን ደጉ!) ቅሌቱ ግን ከቀን ወደ ቀን እያደገ ሄደና በ2008 ዓ.ም ቼን ራሳቸው ከስልጣን ለቀቁ (ተገደው ሳይሆን ወደው!) ከስድስት ወራት በኋላም 3.15ሚ.ዶላር የህዝብ ገንዘብ በመዝረፍና 9ሚ. ዶላር ጉቦ በመቀበል ወንጀል ተከሰው በቁጥጥር ሥር ዋሉ፡፡

በቤተመንግስት ተንፈላሰው ይኖሩ የነበሩት ባልና ሚስት የዕድሜ ልክ እስር (ዓለምበቃኝ!) ተፈርዶባቸው ኑሮአቸውን ወህኒ ቤት አደረጉ፡፡ ከእስሩም በተጨማሪ 15ሚ.ዶላር የገንዘብ ቅጣት ተጥሎባቸዋል (የበሏትን ተፏት!) በኋላ ላይ ግን የዕድሜ ልክ እስሩ ወደ 20 ዓመት ዝቅ ተደረገላቸው፡፡ የሙስና ሽልማቱ እስርና ውርደት ነው - ሁሌም!! በእኛ አገር የተሰራ ጥናት መኖሩን አላውቅም እንጂ የብዙ አገራት ፖለቲከኞች የውድቀት መንስኤ ከሙስና ቀጥሎ የወሲብ ቅሌቶች እንደሆኑ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ (የክሊንተን ትዝ አላችሁ?) የቀድሞው የጣልያን ጠ/ሚኒስትር ሲልቪዮ በርሉስኮኒ “ቡንጋ ቡንጋ” በተሰኘ የወሲብ ቅሌት ይታወቃሉ። በርሉስኮኒ ወደ ሥልጣን ከመምጣታቸው በፊት በጥረታቸው መበልፀግ የቻሉ የቢዝነስ ሰው ነበሩ። አንዴ ስልጣን ላይ ከተፈናጠጡ በኋላም የግል ሚዲያ ተቋማቸውን በመጠቀም ለ17 ዓመት በስልጣን ላይ ለመቆየት ችለዋል፡፡ የበርሉስኮኒ ከፍተኛ ቅሌት የተሰማው በ2011 ዓ.ም ነበር፡፡ ያኔ ነው ለአቅመ ሄዋን ካልደረሰች ኮረዳ ጋር ወሲብ ለመፈፀም ገንዘብ ከፍለዋል በሚል የተወነጀሉት፡፡

ከሞሮኮ አምልጣ ጣልያን የገባችውን የናይት ክለብ ዳንሰኛ በወዳጅነት ይዘዋል በሚል የተወነጀሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤ በ2010 ዓ.ም በስርቆት ወንጀል ተፈርዶባት ወህኒ የወረደችውን እቺኑ ወዳጃቸውን ከእስር አስፈትተዋል - ሥልጣናቸውን ተገን በማድረግ፡፡ ይሄንን እኮ ነው የህግ ባለሙያዎቹ ሥልጣን ያለ አግባብ መጠቀም የሚሉት፡፡ በነገራችሁ ላይ ጠ/ሚኒስትሩ በስልጣን ላይ ሳሉ ሚላን ከተማ አቅራቢያ በሚገኘው የተንጣለለ መኖሪያ ቤታቸው ውስጥ በሚያዘጋጁትና ቆነጃጅት ኮረዶች በሚያደምቁት ፓርቲያቸው (የፖለቲካ ፓርቲ አይደለም!) በእጅጉ ይታወቃሉ፡፡ የሚገርመው ደግሞ ምን መሰላችሁ? ይሄን “ቡንጋ ቡንጋ” የተሰኘ ፓርቲ የማዘጋጀት ሃሳብ ያገኙት ከቀድሞ ወዳጃቸው የሊቢያው መሪ ሙአመር ጋዳፊ ነው ይባላል (ወዳጅ አሳሳተኝ ማለት እኮ አያዋጣም!) ጋዳፊም ራሳቸው ከወጣት ሴቶች አድናቂዎቻቸው ጋር ፓርቲ ያዘጋጁ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በርሉስኮኒ ከስልጣን የወረዱት ገና ክስ ሳይመሰረትባቸው ነው - የዛሬ ሁለት ዓመት፡፡ ከወሲብ ጋር በተያያዙ ወንጀሎችና ሥልጣን ያለአግባብ በመጠቀም ክስ የተመሰረተባቸው የቀድሞው የጣልያን ጠ/ሚኒስትር ጥፋተኛ ሆነው ከተገኙ የ15 ዓመት እስር ይጠብቃቸዋል፡፡

የወሲብ ቅሌትም ውጤቱ ይኸው ነው - ውርደት!! በ2000 ዓ.ም የእስራኤል ፓርላማ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት አድርጐ የሾማቸው ሞሼ ካትሳቭ፣ እንደ ታይዋኑ ቼን ከድሃ ቤተሰብ የወጡ ነበሩ (ሥልጣን እኮ ቤተሰብን ብቻ ሳይሆን አገርንም ያስረሳል!) እኚህ ፕሬዚዳንት በስልጣን ዘመናቸው የቀረቡላቸውን አያሌ የፍርደኞች አቤቱታዎችና የይቅርታ ጥያቄዎች ውድቅ በማድረግ ይታወቃሉ፡፡ ሥልጣን በተቆናጠጡ በስድስተኛ ዓመታቸው ነበር ያላሰቡት ጣጣ የመጣባቸው፡፡ ነገሩን የጀመሩት ደግሞ ራሳቸው ፕሬዚዳንቱ ናቸው፡፡ በ1990ዎቹ የቱሪዝም ሚኒስትር ሳሉ አብራቸው ትሰራ የነበረች ሠራተኛ “እከስሃለሁ” እያለች እንደምታስፈራራቸው ለአቃቤ ህግ ይጠቁማሉ (ዓሳ ጐርጓሪ ዘንዶ ያወጣል አሉ!) በተካሄደው ምርመራም የሴትየዋ ውንጀላ እውነት ሆኖ ተገኘ፡፡ ሞሼ ካትሳቭ፣ ሁለት ጊዜ ሴትየዋን አስገድደው ወሲብ ፈፅመዋል። ሁለት የአስገድዶ መድፈር ወንጀል ማለት ነው። በዚህ ቢያበቃ ጥሩ ነበር፡፡ ሌሎች ሴቶችም ብቅ አሉ። በፕሬዚዳንትነት ዘመናቸው የወሲብ ጥቃት ሙከራ ፈፅመውብናል የሚሉ፡፡ ካትሳቭ ግን ውንጀላውን ካዱ፡፡ “እኔ ሴቶችን ማቀፍና መሳም እንጂ ሌላ ነገር አላደረግሁም” ሲሉ ሸመጠጡ።

(በሳቸው ቤት ማቀፍና መሳም ችግር የለውም!) ክሱ ፖለቲካዊ ሴራ ነው ሲሉም አጣጣሉት፡፡ በ2007 ዓ.ም ከፕሬዚዳንትነታቸው በፈቃዳቸው ለቀቁ፡፡ በመጨረሻም ፍ/ቤቱ ጥፋተኝነታቸውን በማረጋገጡ፤ በሰባት ዓመት እስር እንዲቀጡና ለጥቃት ሰለባዎቹ ካሣ እንዲከፍሉ ተፈረደባቸው። ካትሳቭ በተፈረደባቸው ዕለት የእስራኤል ጠ/ሚኒስትር ቢንያሚን ኔታንያሁ እንዲህ አሉ “የሃዘንና የሃፍረት ቀን ነው!” እውነት ብለዋል! ከዚህ የባሰ ምን ሃፍረት አለ (የአገር ቅሌት እኮ ነው!) አሁን ደግሞ ከእስራኤል ወደ ኡዝቤኪስታን ነው የምናመራው፡፡ ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል በ2012 ዓ.ም ባወጣው ሪፖርት መሰረት፤ እቺ አገር በሙስና ከ174 አገራት 170ኛ ነው የወጣችው (ከሷ የሚብሱት አራት አገራት ብቻ ናቸው!) የኡዝቤኪስታን የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚ/ር የፀረ ሙስና ክፍል ሃላፊ ናስሬዲን ታሊቦቭ ሲናገሩ “ህዝባችን ለማንም ቢሆን ጉቦ መስጠትን ተላምዶታል - ለአስተማሪም ይሁን ለሃኪም ይሰጣል” ብለዋል። ይሄ ስህተት መሆኑኑ መቀስቀስ እንፈልጋለን ያሉት ታሊቦቭ፤ የግልፅነት አለመስፈንና የከፍተኛ አመራሮች እምቢ ባይነት ያንን እንዳናደርግ እንቅፋት ሆነውብናል ሲሉ አስረድተዋል፡፡

የትራንፓረንሲ ኢንተርናሽና ምክትል ማኔጂንግ ዳይሬክቲንግ ሚክሎስ ማርሻል በበኩላቸው፤ ከፍተኛ አመራሮች ምንም ዓይነት ተጠያቂነት የለባቸውም ይላሉ። እንዴት ሲባሉ … “ተቃዋሚ ፓርቲዎች የሉም፤” ሲቪል ማህበራትና ነፃ ፕሬስም በአገሪቱ የሉም” በማለት ያብራራሉ፡፡ አያችሁልኝ … እነዚህ ተቋማት ለፖለቲካዊ ነፃነት ብቻ አይደለም የሚፈለጉት፡፡ ሙስናንም በመከላከል ረገድ ትልቅ ሚና አላቸው። ምናልባት እኮ እኛም አገር ሙስናው የተጧጧፈው እነዚህ ተቋማት በመዳከማቸው ሊሆን ይችላል - ተቃዋሚዎች፤ ሲቪል ማህበረሰቦችና ነፃ ፕሬስ!! (ምን ትላለህ ኢህአዴግ?) በየዓመቱ የዓለም አገራትን የሙስና ደረጃ ይፋ የሚያወጣው ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል፤ የሙስና መጠንን የሚመዝነው በአራት ዋና ዋና ጉዳዮች ነው፡፡ 1ኛ የፖለቲካ መብት 2ኛ. የሲቪል ማህበረሰብ ነፃነት 3ኛ. የፕሬስ ነፃነት 4ኛ. የቢዝነስ አሰራር ግልፅነት … ናቸው፡፡ እነዚህ ነገሮች በቅጡ በተከበሩባቸው አገራት የሙስና መጠን ዝቅተኛ ይሆናል ባይ ነው - ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል፡፡

በዚህ አጋጣሚ የአገራችንን የሙስና መጠን ከእነዚህ መለኪያዎች አንፃር በመመዘን ሃቁን ለራሳችሁ ብትረዱት ሸጋ ነው (ኢህአዴግማ ያውቀዋል!) እንግዲህ የሙስናን ነገር አይደል የምናወጋው። እስቲ የአዲሲቷን አገር የደቡብ ሱዳንን ከፍተኛ የሙስና ሃሜት ልንገራችሁ (ላልሰማችሁ ማለቴ ነው!) የበጀቷን 98 በመቶ በነዳጅ ዘይት ገቢ የምትሸፍነው ደቡብ ሱዳን፤ በቀን ግማሽ ሚሊዮን በርሜል የነዳድ ዘይት ታመርታለች፡፡ እቺ አገር እስከ 2012 ዓ.ም 10ቢ. ዶላር ገቢ ያገኘች ሲሆን ከዚህ ውስጥ 4 ቢ.ዶላር እምጥ ይግባ ስምጥ አይታወቅም። የሚገርመው ደግሞ ምን መሰላችሁ? ነገሩ “የውሾን ነገር ያነሳ” ሆኖ መቅረቱ ነው፡፡ ደቡብ ሱዳን የሙስና ጉዳዮችን የሚመረምር መ/ቤት ቢኖራትም እስካሁን አንድም ባለስልጣን በዚህ ጉዳይ አልተጠየቀም ነው የሚባለው፡፡ (በዚህ ከቀጠለች አገርም የምትሆን አትመስልም!) የሙስና አብዮቱ ይቀጥል! (በዘመቻ ሳይሆን በጥናት!)

ከአዲስ አበባ 135 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው የመተሀራ ከተማ የነዋሪዎች ቁጥር አነስተኛ ነው፡፡ ሆኖም ከተማዋ ጅቡቲን ጨምሮ ከተለያዩ ቦታዎች የሚመጡ መንገደኞችና ሹፌሮች መናኸሪያ ናት፡፡ ከምሽቱ 12፡30 ጀምሮ ከተማዋ ትሟሟቃለች፡፡ ቡና ቤቶችና ጭፈራ ቤቶች ይደምቃሉ፡፡ መተሃራ ህንፃ የበዛባት ከተማ አይደለችም፡፡ በፍራፍሬዎቿ ግን ትታወቃለች፡፡ ሌላው መታወቂያዋ 11ሺ ሠራተኞች ያሉት የመተሃራ ስኳር ፋብሪካ ነው፡፡ ፋብሪካው ለሠራተኞቹ የራሱ የመኖርያ ካምፕ አለው - እንደ ጤና ጣቢያ ያሉ ማህበራዊ አገልግሎቶች የተሟሉለት፡፡

መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፤ ይሄ ካምፕ ትልቅ አደጋና ስጋት ተጋርጦበታል፡፡ ኤችአይቪ በስፋት ተሰራጭቷል፡፡ እማዋይሽ (ሃና) የዛሬ ሰባት ዓመት ናዝሬት ከምትሠራበት የምሽት ክበብ ወደመተሃራ ካምፕ የመጣችው የትዳር ጓደኛ አግኝታ ነው - በጓደኛዋ በሊንዳ አማካኝነት፡፡ ሊንዳ በናዝሬት የምሽት ክበብ ከእማዋይሽ ጋር ትሰራ የነበረች የልብ ወዳጅዋ ስትሆን ከእሷ ሦስት ዓመት ቀድማ ነው መተሃራ የገባችው - ባል አግብታ፡፡ እሷ ከቡና ቤት ህይወት እንደተላቀቀችው ሁሉ ጓደኛዋንም ለማላቀቅ አስባ፣ እማዋይሽን ከባለቤቷ ጓደኛ ጋር አስተዋወቀቻት፡፡ እናም ትዳር ይዛ መተሃራ ከተመች - እማዋይሽ፡፡

ከባሏ ጋር የተስማማችው እሱ በሚሰጣት ገንዘብ ቤታቸውን በማስተዳደር የቤት እመቤት እንድትሆን ነበር፡፡ በጉዳዩ ተስማምታ ወደ ትዳሩ ብትገባም ቅሉ መዝለቅ ግን አልቻለችም፡፡ የጫትና የሲጋራ ሱስ አለባት፡፡ እነዚህን ሱሶቿን የምታረካበት በቂ ገንዘብ ግን በእጇ ላይ ልታገኝ አልቻለችም፡፡ ባለቤቷ ከሚሰጣት የአስቤዛ ወጪ ለሱሷ የሚሆን ገንዘብ ለማትረፍ ብትሞክርም አልሆነላትም፡፡ ገንዘቧ ትንሽ ናት፡፡ ስለዚህም ነው ትታው ወደመጣችው ህይወት ተመልሳ የገባችበት፡፡ ከባለቤቷ ተደብቃ ከስራ ባልደረቦቹ ጋር መማገጥ ጀመረች፡፡ እንዲያም እያለች ለሲጋራና ጫት መግዢያ በቀን ሀያና ሃያ አምስት ብር ድረስ ታገኝ ነበር፡፡

አሳዛኙ ነገር ባለቤቷን ማጭበርበሯ ብቻ አልነበረም፡፡ ጥንቃቄ የጐደለው ወሲብ መፈፀሟም ጭምር እንጂ፡፡ እማዋይሽ ሠባት አመታት በትዳር ስትኖር አጥብቃ የምትመኘው ልጅ የመውለድ ነገር አልተሳካላትም፡፡ ያልሔደችበት ሀኪም ቤት የለም፡፡ ያላማከረችው ሰው የለም፡፡ የማታ ማታ ግን ለምታምነው ታቦት ተስላ ማርገዝ መቻሏን ትናገራለች፡፡ እርግዝናዋ እየገፋ ሲመጣ በህክምና ባለሙያዎች ግፊት የጤና ምርመራ ለማድረግ ተገደደች፡፡ ውጤቱ አስደንጋጭ ነበር፡፡ ቫይረሱ በደሟ ውስጥ እንዳለ ተነገራት፡፡ እውነታውን ለመቀበል ተቸገረች። ሌላ ክሊኒክ ሄዳ ብትመረመርም ውጤቱ ያው ሆነ። የምርመራ ውጤቷን ለማንም እንዳይነግሩባት ለካምፑ የጤና ባለሙያዎች ብትነግርም፣ እማዋይሽ እቤቷ ሳትደርስ ነበር ጐረቤቶቿ ሲያሟት የሠማችው። ለባለቤቷ ውጤቱን ማርዳት አስፈርቷት ሳትነግረው ወንድ ልጅ በሰላም ተገላገለች፡፡ ልጁ ግን ጤነኛ አልነበረም፡፡

የኤችአይቪ ቫይረስ በደሙ ውስጥ ነበረበት፡፡ የልጁ ጤንነት ማጣት ያሳሰበው ባሏ ነው ህፃኑን ወደ ጤና ጣቢያ ወስዶ ያስመረመረው፡፡ ከጤና ጣቢያው ሲመለስ “አንቺ ሸርሙጣ፤ ልጄን ገደልሽው” ብሎ አምባረቀባት፡፡ ልብሶቿን አውጥቶ በመወርወር ድምፅ ሳታሠማ ከቤቱ እንድትወጣለት አዘዛት፡፡ ትኩስ አራስ የነበረችው እማዋይሽ፤ የባሏ እግር ላይ ወድቃ እንዳያባርራት የሙጥኝ አለችው፡፡ ይቅርታ እንዲያደርግላት ተማጠነችው፡፡ ሁለቱም የመጣባቸውን መከራ በጋራ ተቀብለው አብረው እንዲኖሩ ለመነችው፡፡ ይሄኔ ነው ቱግ ብሎ ሃቁን የነገራት “አንቺ ነሽ መከራ ያለብሽ እኔ ነፃ ነኝ፣ ባንቺ ቤት እኔን የጐዳሽ መስሎሻል፤ ልጄን ግን በላሽው” በማለት የተመረመረበትን ወረቀት አሳያት፡፡ ለካስ እሱ ከቫይረሱ ነፃ ነው፡፡

ይሄኔ ምንም ሳታመነታ ልብሷን ሰብስባ ከቤት ወጣች፡፡ ግን ወዴት እንደምትሔድ አታውቅም ነበር፡፡ አንድ ሳምንት ልጇን ይዛ ጓደኛዋ ጋር ተቀመጠች፡፡ ልጇም በወር ከ15 ቀን ዕድሜው ህይወቱ አለፈ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ነው እማዋይሽ መተሃራ መናኸሪያ ጐን ካለ አንድ የማንጐ ዛፍ ስር ላስቲክ በመወጠር የጐዳና ኑሮዋን አንድ ብላ የጀመረችው፡፡ በዚህ ቦታ መኖሯን የምታውቀው ብቸኛ ጓደኛዋ ሊንዳ ነበረች፡፡ እየመጣችም ትጠይቃታለች፡፡ አንድ ቀን ግን ሊንዳ ፀጉሯን አንጨባራ ባዶ እግሯን እንደ እብድ እየሮጠች እማዋይሽ ጋ ትመጣለች፡፡ “ምን ሆነሽ ነው?” ትላታለች፡፡ “ጐሹ” “ጐሹ” ብቻ ነበር የምትለው - ሊንዳ፡፡ ጐሹ ባለቤቷ ነው፡፡ በአንድ ድርጅት ውስጥ ሥራ ለመቀጠር የጤና ምርመራ አድርጐ፣ የኤች አይቪ ኤድስ ቫይረስ በደሙ ውስጥ መኖሩ ሲነገረው፣ በሽታውን ያመጣችበት ሚስቱ እንደሆነች ቅንጣት አልተጠራጠረም፡፡

ለዚህም ነው ቤት እንደገባ ዱላ የጀመረው፡፡ ይሄኔ አምልጣ ወደ ብቸኛ ጓደኛዋ እማዋይሽ መጣች፡፡ ነገሩ ለእማዋይሽ አስደንጋጭ ነበር፡፡ ለአንድ ቀንም ቢሆን ከሊንዳ ባል ጋር መተኛቷን ታውቃለች። ክፉኛ አዝና ብታቀረቅርም ከባሏ ጋር መማገጧን አልተናዘዘችላትም፡፡ ሊንዳ በነጋታው ወደ ጤና ጣቢያ ትሄድና ምርመራ ታደርጋለች፡፡ ያልተጠበቀ ነበር ውጤቱ፡፡ ከቫይረሱ ነፃ ነሽ ተባለች፡፡ ከዚህ በኋላ ሊንዳ ጓደኛዋን ራቀቻት፡፡ ሁለቱ የነፍስ ጓደኛሞች ዳግም ላይገናኙ ተለያዩ፡፡ እማዋይሽ ምክንያቱን ባታውቀውም፡፡ ዛሬ እማዋይሽን ከህመሟ በላይ የሚያሠቃያት ልጇን ከቫይረሱ ነፃ ማድረግ እየቻለች ለህልፈት መዳረጓ ነው፡፡ የእግር እሳት የሆነብኝ የልጄ ነገር ነው ትላለች፡፡ ልጄ ቢኖር ኖሮ መፅናኛዬ ይሆነኝ ነበር በማለት ሀዘኗን በእንባ ትገልፃለች፡፡

ሌላው ውስጧን እያመሰ የበጠበጣት ደግሞ በጓደኛዋ ላይ የፈፀመችው ክህደት ነው፡፡ ከገዛ ጓደኛዋ ባል ጋር ተኝታ በሽታውን በማስያዝ ትዳር ማፍረሷ በፀፀት ያንገበግባታል፡፡ የራሷ ሳያንስ የጓደኛዋን ህይወት መበጥበጧ መልሶ ይበጠብጣታል፡፡ “መሞት ስለምፈልግ የፀረ- ኤችአይቪ መድሃኒቱን አልጠቀምም” ትላለች ተስፋ በቆረጠ ስሜት፡፡ አሁን እማዋይሽ ደካክማለች፡፡ ፊቷ እና እጆቿ ቆሳስለዋል። የእነዚህ ጓደኛሞች አሳዛኝ ታሪክ ማለቂያ ያለው አይመስልም፡፡ ሊንዳ የእማዋይሽን የቀድሞ ባል አግብታ እየኖረች ነው - ራሷ እማዋይሽ እንደነገረችኝ፡፡ እሷ ግን ሞቷን ትጠባበቃለች፡፡ አሳዛኝ የህይወት ክስተት ይሏል ይሄ ነው!!

Published in ዋናው ጤና

ዴሞስቴን የተባለ የግሪክ ደስኳሪ፣ በታሪክ አንደበተ-ርቱዕ ከሚባሉት አንዱ ተደናቂ ፈላስፋ ነው! ዴሞስቴን አያሌ ጊዜ ለአቴና (ግሪክ) ህዝብ ንግግር አድርጓል፡፡ ንግግሩ ተደማጭ ይሆን ዘንድ አንደበቱን ለመግራት፣ ምላሱን ለማስላት፣ ወንዝ ወርዶ ከምላሱ ሥር ጠጠር እያደረገ ከወንዙ ጅረት ጋር የሚፎካከር የጩኸት ድምጽ በማውጣት የአንደበት አቅሙን አካብቷል፡፡ እንግዲህ፤ ዴሞስቴን በተደጋጋሚ የአቴና ህዝብ ወራሪዎች እየመጡበት መሆኑን ተናግሮ የሚሰማው አጥቷል፡፡

በመጨረሻም፤ ህዝብ በተሰበሰበበት ቦታ ሄዶ መድረኩ ላይ ወጥቶ መናገር ጀመረ፡፡ “አንድ ተረት ብነግራችሁ ለመስማት ዝግጁ ናችሁ?” ሲል ጠየቀ፤ ደስኳሪው ዴሞስቴን፡፡ “አዎ!” አለ ህዝቡ፡፡ (ተረት የማይማርከው ህዝብ የለም፡፡) “አንድ አህያ የሚያከራይ ሰው ነበር” ሁላቸውም ጆሮአቸውን ወደ ባለ አህያውና አህያው ታሪክ አቀኑ፡፡

“አንድ አህያ ተከራይ መጥቶ፤ የበረሃ ጉዞ ስላለብኝ፤ አህያህን አከራየኝ?” አለው ለባለአህያው፡፡

“እሺ፤ እንስማማ?!”

አለው አከራይ፡፡ ተስማሙና አህያውን ይዞ ሄደ፡፡ በነጋታው የበረሃ መንገዱን ተያያዘው፡፡ እንዳጋጣሚ የአህያው አከራይም ወደዚያው በረሃ ይሄድ ኖሮ መንገድ ላይ ተገናኙ፡፡ አብረው መጓዝም ቀጠሉ፡፡

ቀትር ላይ ደከማቸውና ጭው ባለ በረሃና ቃጠሎ፤ ሆጨጭ ባለው አሸዋ ላይ እረፍት አደረጉ፡፡ በአህያዋ ጥላ ሥር የተከራየው ሰው አረፍ አለ፡፡ ይሄኔ ባለ አህያው፤ “አህያዋን እንጂ ጥላዋን አላከራየኸኝም ተነስ” አለና ሙግት ጀመረ፡፡ ተከራዩ ደግሞ፤ “አህያዋን ስከራይ በአህያዋ በኩል የሚመጣ ጥቅም ሁሉ የእኔ ነው” አለ፡፡ ሙግቱ ተፋፋመ፡፡

ዴሞስቴን ወደ ህዝቡ ዞሮ፤ “እህስ፤ ጥላው የማነው?” ሲል ይጠይቃል፡፡ ከፊሉ ህዝብ፤ “የባለ አህያው ነው!” ሲል ጮኸ፡፡ ከፊሉ “የተከራዩ ነው!” ሲል ጩኸቱን አሰማ፡፡ ከፊሉ ደግሞ፤ “አዲስ ድርድር ያሻል!” አለ፡፡ ከፊሉ፤ “ዳኛ ጋ ይሂዱ!” አለ፡፡ ይሄኔ ዴሞስቴን፤ “የአቴና ህዝብ ሆይ! አሳሳቢውን የሀገራችንን መወረር ነገር ስነግራችሁ ጆሮአችሁን አልሰጥ አላችሁኝ፡፡ የአንዲት አህያ ጥላ ታሪክ ግን ይህን ያህል አጯጯሃችሁ! እጅግ ታሳዝናላችሁ!”

ብሏቸው ሄደ፡፡ ህዝቡም፤ “ታሪኩን ጨርስልን! መጨረሻቸው ምን ሆነ?”

እያለ ጩኸቱን ቀጠለ፡፡ ዴሞስቴን ግን መንገዱ ቀጠለ፡፡

                                                         * * *

የምንጮህበትን እንወቅ፡፡ የሀገር ጉዳይ፣ የሥርዓቱ ጉዳይ፣ የፓርቲ ህግጋትና አካሄድ ጉዳይ፤ ምኑ ቅጡ … ትላልቁ ስዕል እያለ፤ በትናንሽ የካርቱን ስዕሎች መታለል የለብንም፡፡ ከዚያ ይሰውረን! ሥጋታችን፤ የሥልጣን ገዋ (Power vacuum) እንዳይፈጠር እንጂ፤ የሰው ገዋማ ችግር የለም፡፡ ማንም ይተካል፡፡ የተንሳፈፈ የፖለቲካ አቅጣጫ፤ አሳሳቢ ነው፡፡ በጥቃቅን ነገር ላይ እንድናተኩር ያደርጋል፡፡ ያዘናጋል፡፡ በማናቸውም ዕምነት ላይ አምላኪ እንድሆንና እንድናተኩር፣ እንድንጨቃጨቅም ያደርጋል፡፡ ኦባማ፤ “ህዝባችን በሀገር ውስጥ ገቢ ላይ ዕምነቱን እንደገና እንዲያዳብር እናድርግ” አለ አሉ፡፡ ለካ ያሜሪካ ጉዳይ እንደኛ ነው፤ ብንል ማን ይከለክለናል? ግን ያ ተቋም ብቻ ነው ተጠያቂው ሥርዓቱም? ብንልም ያባት ነው፡፡ ከላይ የጠየቅነው ዴሞስቴን የአቴናን ንጉሥ ሲሞግት፤ “በፈቃዱና አውቆ ስህተት የሚሠራ አለን? ያ ከሆነ ሰውየው የሚያናድድና ለቅጣት የሚዳረግ ነው፡፡ ሆነ ብሎ ሳይሆን ሳያውቅ ስህተት ቢሠራስ? እሱ መቀጣት ሳይሆን ይቅርታን ሊያገኝ ይችላል፡፡

ስህተት የፈፀመውም ሆነ ጥፋት የሠራው በሥራው ተመስጦ፣ ካለማስተዋል የተነሣ ቢሆንና ስኬት የእሱ ባትሆንስ?!” በለስ ያልቀናውን ሰው አናዝንበትም፤ አናጠቃውምም፡፡ አብረነው እናዝናለን እንጂ፡፡ ይሄ ሁሉ በእኛ ህግ ጥላ ሥር የሚፈረድ ብቻ አይደለም፡፡ የለም፤ ተፈጥሮ፤ ባልተፃፈ ህግዋ ያስቀመጠችው ነው። ህገ-አዕምሮ የሚዳኘው ነው፡፡ ስለዚህ ኤስፒለስ (ዴሞስቴን በህዝብ ጥያቄ የሽልማት ዘውድ ይጫንለት የተባለውን ሃሳብ የተቃወመው ንጉሥ፣ በእስተዛሬው አገዛዙ፤ በጭካኔውና በግፉ ሰውን ሁሉ በመብለጡ፣ እንደክፉ -ዕጣ ፈንታ የዘረዘራቸውና እኔን የከሰሰባቸው በሙሉ የራሱ መጠየቂያ ናቸው…” ይልና ኦ ደጉ ባለሞገሱ አምላክ ሆይ! እባክህ ምህረትህ አይለያቸው! እነሆ ለእኒህ ሰዎች የተሻለ መንፈስ፣ የተሻለ ስሜት ስጣቸው፡፡

ሆኖም ጨርሶ የማይድኑ ከሆነ፤ እነሱው በእነሱው ላይ በባህርም በየብስም፣ ያለወቅቱ የመጣ መርገምትንና የመንፈስ መንኮታኮትን፤ ይፈርዱ ዘንድ ተዋቸው፡፡ እኛም የተረፍነው በደግነትህ ደህንነት፣ ቸርነትህን ለተጐናፀፍነውና ካሰፈሰፈው መዓት በማያወላውል መልኩ በፈጣሪ እርምጃ እንድን ዘንድ ለታደልነው፤ ከዚህ የማስጠንቀቂያ ደወል በኋላ፤ ፀጋህን አላብሰን፡፡” ስለ ሥርዓት ስናስብ የካምቦዲያው አብየታዊ መሪ ሲሞን ቦሊቫር “በፍፁም ሥልጣን የናጠጡ ገዢዎች ሥር መኖር፤ ለማናቸውም ሹም ያላንዳች ተቃውሞ አሜን ብሎ መኖር ነው፡፡ የጨቋኙ ገዢ ፍቃደ - ልቡና የላዕላይ ህጉ የበታች ሹማምንት እንደልብና በዘፈቀደ በተደራጀ የጭቆና ስልት እንዲበዘብዙ የሚፈቅድላቸው፤ መሆኑን ልብ እንበል ይለናል፡፡

ቦሊቫር፣ ለኮንግሬሱ ባደረገው ንግግር ፓርላማውን ሲያስጠነቅቅም “ነፃነታችንን ማስጠበቅና ማቆየት አዳጋች ነው፡፡ ምክንያቱም አንድም ሦስትም የሆኑት ሦስቱ ዋና ዋና ጠላቶቻችን፣ ማለትም ድንቁርና፣ ጭቆናና ሙስና (Triple yoke of Ignorance, Tyranny and corruption) የህዝቡን ዕድገት ስላቀጨጩት ነው! እንዳሻቸውም ሁሉን እንዲከውኑ ይፈቅድላቸዋል፡፡ ባርነት የጨለማ ሴት - ልጅ ነው፡፡ ዕውር ህብረተሰብ የገዛ መንኮታኮቱ ዕውር መሣሪያ ነው፡፡ ክፉ ምኞትና ክፉ ሴራ የህዝቡን ዝግጁ አማኝነትና ልምድ - አልባነት በመንተራሱ ጥቅም አካብተውለታል። ከቶውንም የፖለቲካዊ፣ ኢኮኖማያዊ ወይም የሲቪል የመረዳት - አቅም - ማጣት ህዝቡን ለዚህ ዳርጎታል፡፡ ውዥንብሩን፣ ድንግርግሩንና ቅዠቱን ሁሉ ዕውነታ ነው ብሎ ማሰብ፤ ማንኛውንም ዓይነት ሊቼንሣ፤ ከነፃነት ጋር ማምታታት፤ ሀገር መክዳትን በጀግንነት ስም ማወጅ፣ ፍትህን የበቀል ካባ ማልበስ ሆኗል ዘመናዊው ሥልጣኔ፡፡ “ነፃነት”፣ ይላል ሩሶ፤ “እጅግ በጣም ምርጥና ምራቅ የሚያስመጣ ምግብ ያለበት ቢፌ ነው፡፡ ሆኖም ጥሩ አርጐ ፈጭቶ ከሰውነት ለማዋሃድ እጅግ አዳጋች ነው፡፡

ይለናል፡፡ አንድ ዕውቅ - ሌባና አጭበርባሪ ሹም፤ ዴሞስቴንን፣ “ለሊት በሻማ እየፃፈ ቁጭ ብሎ ያድራልና ሊከለከል ይገባል”፤ ሲል ከሰሰው፤ ይባላል፡፡ ዴሞስቴንም፤ “አዎን በቅጡ የማውቀው አንድ ነገር አለ፡- ብርሃን ሁሉ ከአገር ቢጠፋ አንተ ደስታህ ነው፡፡ ለስርቆት የሚመችህ ያኔ ነዋ! እላንት የአቴና ህዝቦች ሆይ! አይግረማችሁ! እስከዛሬ ከታዩት ያገር ካዝና ዘረፋና ሌብነቶች ሁሉ፤ ያሁኑ አያስደንቅም፡፡ ምክንያቱም ሌባው ሁሉ የተሠራው ከነሐስ ነው፡፡ አገሩ የተሠራው ግን ከሸክላ ነው፡፡

ማንኛቸው እንደሚፈርሱ እናንተ ለዩ!” አለ፡፡ ትናንሽ ዕድሎችና ቀዳዳዎች፤ አብዛኛውን ጊዜ የታላላቅ ገንዘብ - ማፍሪያ ኢንተርፕራይዞች ምንጮች (መነሻዎች) ናቸው፡፡ ምንጮቹ የሚደፈኑት ሥርዓቱ አይቷቸው ራሱን ሲመረምር ነው!! ይላሉ ሌሎች ፀሐፍት፡፡ ችግሩ፤ “ሌባው ሁሉ የተሠራው ከንሐስ ነው፡፡ አገሩ የተሠራው ግን ከሸክላ ነው!!” በሼክስፒር ድርሰት ብሩተስና ግብረ-አበሮቹ በህብረት ንጉስ ጁሊየስ ቄሣርን በጩቤ ጠቅጥቀው በገደሉት ወቅት፤ የልብ ወዳጄ የሚለው ብሩተስ እንደወጋው ያየው ሟቹ ቄሣር “አንተም ብሩተስ?

(eftu Brute?) እንዳለው ይታወሳል፡፡ ቀጥሎ ከወጊዎቸ አንዱ ባለሟል የጠየቀውም አይረሴ ነው፡- “ቀጥሎ ምንድን ነው ሥራችን?!” (በገነነ ቃለ-አንክሮና በደም ጉምዥት)

Published in ርዕሰ አንቀፅ

“የሚገጥመኝ እንግልት ብዙ ነው”

በአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያውን የመፃሕፍት መሸጫ መደብር በመክፈት የሄዶን ዜግነት የነበራቸው ሚስተር ዴቪድ ቀዳሚ ሲሆኑ፤ መፃሕፍት አዙሮ በመሸጥ ደግሞ ተስፋ ገብረሥላሴ መሆናቸውን “ዘመን ተሻጋሪ ባለውለታ” የተባለው መጽሐፍ ይጠቁማል። ከአንድ ክፍለ ዘመን በላይ ባስቆጠረው የመፃሕፍት ዝግጅት፣ ህትመትና ስርጭት ዙሪያ ካሉ ያሉ ችግሮች ዛሬም ድረስ አልተፈቱም፡፡ በጐዳና የመፃሕፍት ንግድ ሥራ ላይ የሚገኘው ወጣት ድንቁ ግርማ የሚደርስበት እንግልት ለዚህ ምሳሌ ሆኖ ሊቀርብ ይችላል። የአምስት ዓመታት የመጽሐፍ ንግድ ሥራ ሂደቱና የሕይወት ውጣ ውረዱን አውግቶኛል፡፡

የእግር ጉዳትህ የተፈጥሮ ነው?

አይደለም፡፡ ጤናማ ሆኜ ነው የተወለድኩት። ወላጆቼ እንደነገሩኝ ከሆነ የ3 ዓመት ልጅ እያለሁ ወድቄ፤ በወቅቱ ወደ ሐኪም ቤት ስላልተወሰድኩ ለእግር ጉዳተኛነት ተዳረግሁ፡፡ ትውልድህና ዕድገትህ የት ነው? በ1980 ዓ.ም በሱሉልታ መንደር ነው የተወለድኩት፡፡ ሦስት እህትና ሁለት ወንድሞች አሉኝ፡፡ እኔ የመጀመሪያ ልጅ ነኝ፡፡ በሱሉልታ ብዙ አልቆየሁም፡፡ ደብረብርሃን (ደነባ) ሄጄ ከዘመድ ጋር ስድስት ዓመታት ኖሬያለሁ፡፡ ከዚያ ጠፍቼ በመምጣት በአዲስ አበባ በጐዳና ተዳዳሪነት ሁለት ዓመታት ያህል ቆይቻለሁ፡፡ ከጐዳና ተዳዳሪነት መውጣት እንዴት ቻልክ? መርካቶ ሃብተጊዮርጊስ ድልድይ አካባቢ ነበር የማድረው፡፡ አድራሻው እንቁላል ፋብሪካ አካባቢ የሆነ “ሲዳርታ” የሚባል የበጐ አድራጐት ድርጅት ከጐዳና አንስቶ ወደ ማዕከሉ አስገባን፡፡

ከትምህርት ጋር ለመጀመሪያ ጊዜ የተገናኘሁት እዚያ ነው፡፡ በማዕከሉ አራት ዓመት ስቆይ ደብል እየመታሁ 6ኛ ክፍል ደርሻለሁ፡፡ ሰርከስ ሊያሰለጥኑን ሞክረዋል፡፡ የእንጨትና የብረታ ብረት ሥራም አስተምረውናል። ከዚያ በኋላ ራሳችሁን ቻሉ ተብለን ተሰናበትን፡፡

ቀጣይ የሕይወት አቅጣጫህ ምን ሆነ?

በእንጨትና በብረታ ብረት ሥራ ተቀጥሬ ለመሥራት የተለያዩ ቦታዎች ሄጄ ብጠይቅም የሚቀበለኝ አጣሁ፡፡ ከሲዳርታ ማዕከል ስሰናበት ዊልቸር (ብስክሌት) እና 600 ብር ተሰጥቶኝ ስለነበር በዚያ ካፒታል ሶፍት፣ ማስቲካና ከረሜላ እያዞርኩ መሸጥ ጀመርኩ፡፡ መጽሐፍ አዙሮ የሚሸጥ ጓደኛዬ ከዚህ ሥራ ጋር አገናኘኝ፡፡ ፒያሳ ጐዳና ላይ መጽሐፍ በመሸጥ አምስት ዓመታት አስቆጥሬያለሁ፡፡ የመፃሕፍት ንግድ እንዴት ነው? ሥራው ጥሩ ነው፡፡ የመፃሕፍት ሕትመት ቁጥር ብቻ ሳይሆን አንባቢም እየጨመረ ነው፡፡ የመፃሕፍት ዋጋ እየተወደደ ቢመጣም ሕዝቡ የማንበብ ፍላጐት እንዳለው ይታያል፡፡

የአንባቢያን የመፃሕፍት ምርጫ ምን ይመስላል?

ምርጫው እንደየሰው ፍላጐት የሚለያይ ነው። የፍቅር፣ የፍልስፍና፣ የታሪክ፣ የሳይኮሎጂ…መፃሕፍትን ሰው እንደየፍላጐቱ ነው የሚገዛው፡፡ አንተስ ታነባለህ?

የመጽሐፍ ምርጫህስ ምንድነው?

የማንበቡ ፍላጐት አለኝ፡፡ ግን የሥራዬ ባህሪና ያለብኝ የሥራ ችግሮች እንደምመኘው ለማንበብ አላስቻለኝም፡፡ ከጠዋቱ 2 ሰዓት እስከ ምሽቱ 3 ሰዓት ድረስ ነው የምሰራው፡፡ የጐዳና ላይ ነጋዴ ስለሆንኩ በየዕለቱ ከፖሊስ፣ ከሕግና ደንብ አስከባሪዎች ጋር ጭቅጭቅ ነው፡፡ ብዙ መንገላታትና በተለያዩ ጊዜያት የንብረት መወረስም ገጥሞኛል፡፡ በአንድ ወቅት 7ሺህ ብር የሚገመት መፃሕፍት ወስደውብኝ እንዲመለስልኝ በተደጋጋሚ ባመለክትም የሚሰማኝ አላገኘሁም፡፡ የሚገጥመኝ እንግልት ብዙ ነው፡፡ በቅርቡ በእኔ እርዳታ ስር ያሉ እህቶቼን ከተረጂነት ወጥተው ራሳቸው እንዲችሉ 10ሺህ ብር የሚያወጣ የተለያዩ ቁሳቁስ ገዝቼላቸው ከእኔ ጋር ቁጭ ብለው እንዲሰሩ አድርጌ ነበር፡፡ እሱም በሕግና ደንብ ሰዎች ተወሰደባቸው፡፡ እህቶቼ ተመልሰው ወደ ቤት በመግባት የእኔን እርዳታ ጠባቂዎች ሆነዋል፡፡ ቀበሌ በአነስተኛና ጥቃቅን እንዲያደራጅህ እና የመሥሪያ ቦታ እንዲሰጥህ አልጠየቅህም?

እናደራጃችኋለን ይላሉ፡፡ ሄደን ስንጠይቅ የሚያስተናግደን የለም፡፡ ዛሬ ቃል ገብቶልን ተስፋ ሰጥቶን ያነጋገረን ኃላፊ፣ በማግስቱ ስንሄድ በሌላ ሰው ተተክቶ ይገጥመናል፡፡ ዋና የሚባሉትን ኃላፊዎች ለማነጋገር ደግሞ እንከለከላለን፡፡ ስለዚህ ወደ ቀበሌ ለመሄድ ማሰቡ ራሱ ያስጠላል፡፡ የድካሜ ውጤት የሆነውና በሕግና ደንብ ሰዎች የተወረሰብኝን መፃሕፍት እንዲመለስልኝ ስጠይቅ “የሌላ ሰው ሥራ ነው የያዛችሁት” የሚልና አካል ጉዳተኞች መሥራት አይችሉም ብለው እንዲያምኑ ለመረዳት ችያለሁ፡፡

በአካል ጉዳተኝነትህ ልዩ ማበረታቻ አግኝተህ አታውቅም?

መንግሥት ለአካል ጉዳተኞች ልዩ ማበረታቻ ያደርጋል ሲባል ከምሰማው ውጭ እኔ እስካሁን ያየሁትም ሆነ ያገኘሁት ነገር የለም፡፡ የአካል ጉዳተኝነት ልዩ ተጠቃሚነቱ ቀርቶ እንደ ዜጋ ለጠየቅነው የመደራጀትና የመሥሪያ ቦታ ጥያቄ ምላሽ ባገኝ እንዴት ጥሩ በሆነ ነበር፡፡ ጥያቄያችንን ለቀበሌው ብቻ ሳይሆን ለክፍለ ከተማው ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ብናስገባም ሰሚ የለም፡፡ የአካል ጉዳተኞች ማህበር አባል ነህ? የብሔራዊ አካል ጉዳተኞች ማህበር አባል ነኝ፡፡ ዓመታዊ ክፍያ አስከፍለው መታወቂያም ሰጥተውኛል፡፡ ለአንድ ሺህ አካል ጉዳተኞች ኮንዶሚኒየም ቤት በቅድሚያ ይሰጣል ብለውን ገንዘብ ከፍለን ነበር፡፡ እስካሁን ምንም ያገኘነው ነገር የለም፡፡ ከሌላው ጊዜ በተለየ የጎዳና ላይ የመፃሕፍት ንግድ ምን ችግሮች አሉበት? ክረምት ተማሪዎች ከትምህርት የሚያርፉበት ወቅት ስለሆነ የመጽሐፍ አንባቢያን ቁጥር ይጨምራል፡፡ ክረምት ለመፃሕፍት ሽያጭ ጥሩ ጊዜ ቢሆንም በየዕለቱ ጎዳና ላይ የዘረጋናቸውን መፃሕፍት ከዝናብ ለመከላከል የምናደርገው ትግል ከባድ ነው። መፃሕፍቱን ከታች በጎርፍ፣ ከላይ ከዶፍ መከላከሉ አስቸጋሪ ነው፡፡ መፃሕፍት ማሳደሪያ ቦታ የለኝም፡፡ እዚሁ አካባቢ ያሉ ዘበኞች እንዲጠብቁልኝ አደራ ሰጥቼ ነው ወደ ቤት የምሄደው፡፡ ሌሊት ዶፍ ሲወርድባቸው ከተሸፈኑበት ላስቲክ ውጭ መከላከያ የላቸውም፡፡

አሁን ከማን ጋር ነው የምትኖረው?

ብቻዬን የግለሰቦች ቤት ተከራይቼ ነው ያለሁት። በዚህ ሥራ ራሴን ብቻ ሳይሆን እናቴንና እህት ወንድሞቼን እረዳለሁ፡፡ የቤቱ ታላቅ ልጅ በመሆኔም ታናናሾቼን የማገዝ ኃላፊነት እንዳለብኝ ይሰማኛል፡፡ በየዕለቱ በሥራው ላይ የሚገጥሙኝ ችግሮች ሕይወቴ በሥጋት እንዲወጠር ያደርገዋል።

ይህን ሥራ ባጣ እንዴት መኖር እችላለሁ?

የቤት ኪራይስ ምን እከፍላለሁ? እያልኩ እጨነቃለሁ፡፡ ተረጋግቼ ውዬ የማድርበት ቀን የለም፡፡

ቀጣይ የሕይወት ዓላማህ ምንድነው?

ተረጋግቼ ሥራዬ የምሰራበት ቦታ፣ የራሴ ቤትና ትዳር እንዲኖረኝ እፈልጋለሁ፡፡ መንግሥት ለዜጎች፣ ለወጣቶች፣ ለአካል ጉዳተኞች … ያስቀመጣቸውን መብቶች ተግባራዊ ሲያደርግ የእኔም ምኞት በፍጥነት ይሳካል ብዬ አምናለሁ፡፡ ስለዚህ ነገር በየሚዲያው ብቻ ማውራት ጥቅም አይኖረውም። ልመና ይቁም፤ ሥራን እናበረታታ እየተባለ ብዙ ይነገራል፡፡ ሲሆን የሚታየው ግን ከዚህ ተቃራኒ ነው፡፡ እኔ በግሌ በልመና መተዳደርን አልፈልግም፤ ሠርቶ የመኖር ብቻ ሳይሆን የማደግ ከፍተኛ ፍላጎት አለኝ፡ የፈለገ ችግር ቢገጥመኝ ሠርቼ ለመኖር መታገሌን አላቋርጥም፡፡ በመጨረሻ የምታነሳው ሀሳብ ካለ … ጤናማ ሆነውም ይሁን በአካል ጉዳተኝነት፤ በጎዳና ተዳዳሪነትና በልመና የሚኖሩ፤ ሥራ ፈጥረው ለመኖር ቢሞክሩ ከራሳቸው ባለፈ ሌላውን ሊረዱ ይችላሉ፡፡ ሠርቶ ለመኖርም ቢሆን ችግሮች እንዳሉ እኔ በራሴ ልምድ አይቻለሁ፡፡ ፖሊስ ወይም የቀበሌ ሕግና ደንብ ሰዎች መፃሕፍቶቼን በማንገላታትና በመውረስ ሲያንገላቱኝ በተቃራኒው ሕብረተሰቡ “ሠርቶ ይኑርበት” ብሎ ሲሟገትልኝ አይቻለሁ፡፡ ስለዚህ ለምኖ ከመኖር ሠርቶ ማደር እንደሚያስከብር አረጋግጫለሁ፡፡ ሌሎችም እንዲሰሩ አበረታታለሁ፡፡

Published in ህብረተሰብ

ከአዘጋጁ

የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ በፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም “መክሸፍ እንደኢትዮጵያ ታሪክ” መፅሃፍ ላይ የላኩልን ዳሰሳና ትንተና ቀደም ሲል ካስተናገድናቸው ፅሁፎች በአቀራረብና በጥልቀቱ ለየት ያለ በመሆኑ ለአንባቢያን አቅርበነዋል፡፡ ኦሪጂናል ፅሁፉ በጣም ረዥም በመሆኑ ከቦታ ውስንነት አንፃር ዋና ሃሳቡን ሳናጓድል በመጠኑ እንደቀነስነውና ኤዲት እንዳደረግነው ለአንባቢያን ልንገልፅ እንወዳለን፡፡ በዚህ አጋጣሚ ለፅሁፉ አቅራቢ ልባዊ ምስጋናችንን እናቀርባለን፡፡ ፕሮፌሰር መስፍን በተለያዩ ስርዓቶች ሥልጣንን በአደባባይ በመሞገትና “በመጎንተል” የዕድሜያቸውን አብዛኛውን ክፍል አሳልፈዋል። ባለፉት ሃያና ሠላሳ ዓመታት በተለይ እጅግ የሚታወቁባቸውን የጂኦግራፊና የችጋር ጥናቶች ጨምሮ በፖለቲካ፣ በታሪክ፣ በስነ-ጥበብ እንዲሁም በሌሎች ፈርጀ-ብዙ የማህበራዊ ሳይንስ መስኮች በርካታ ሥራዎችን አበርክተውልናል፡፡ ይህም በሀገሪቱ ከታዩት ፅሑፍ አምራቾች/prolific writer/ ተርታ በግንባር ቀደምትነት ያስቀምጣቸዋል፡፡

ፕሮፌሰሩ ክፉኛ በይሉኝታና በፍርሃት በተሸበበች ሀገር፣ በልባቸውና በአእምሯቸው መሐል ሕሊናቸውን የሚያዙና ያመኑበትን በድፍረት ከመተቸት ወደ ኋላ የማይሉ ጉምቱ ምሁር ናቸው። በግሌ እስካሁን ካነበብኳቸው መፃህፍት የሳቸውን መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ ያህል በእጅጉ የኮረኮረኝና ጥያቄ ያጫረብኝ መፅሃፍ አላገኘሁም፡፡ በእርግጥም የፕሮፌሰሩ ስራ እስካሁን በሌሎች የሀገሬ ፅሑፎች ላይ ያልተስተዋለ ትኩረትና አነጋጋሪነትን ማግኘት ችሏል፡፡ ለምሳሌ “መክሸፍ” የሚለው ቃል በአጭር ጊዜ ውስጥ የዕለት ተዕለት ወጋችን አካል ሊሆን በቅቷል፡፡ መፅሐፉን አስመልክቶም በዛ ያሉ የትችት እና የዳሰሳ መጣጥፎች ቢቀርቡም ከተወሰኑት በቀር ይህ ነው የሚባል ጠለቅ ያለ ዳሰሳዊ ምልከታ አልተደረገም።

በተለይ የታሪክ ፍልስፍናውን፣ የሥልጣኔ ሀልዮቱን፣ መክሸፍን እና ውድቀትን እንዲሁም ሌሎች በመፅሀፉ በዝርው የተገለፁ ነገር ግን ትንተና የሚጠይቁ እና ከፍ ያለ ምልከታን የሚሹ ፅንሰ-ሃሳቦች - ስለተቋማት ግንባታ፣ ስለባህል፣ ስለኢትዮጵያዊ የእጣፈንታ ጥያቄ፣ ስለመንፈስ እና ሌሎች ጉዳዮች አልተዳሰሱም። የዚህ ፅሑፍ ዓላማ ሙሉ መፅሐፉን መዳሰስና መገምገም ሳይሆን የታሪክ ፍልስፍናቸውንና በተለይ የመክሸፍ ኃልዮትን ከሌሎች ተጠቃሽ የምዕራባውያን ጥናቶችና ዘመናዊው አስተሳሰብ አንፃር በአመክንዮ በመመዘን እይታቸውን ማጉላትና ውስንነቶቻቸውን በተወሰነ መልኩ ማሳየት ይሆናል፡፡ አጠቃላይ ቅኝት የፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ /2005 ዓ.ም/ የተሰኘው መፅሐፍ ያነሳው ርዕሰ-ጉዳይ ግዝፈት እና የሃሳቡ ይዘት እጅግ ተንኳሽ /polemical/ መሆን ከተለመደው የታሪክ አቀራረብ እና መወድሳዊ የታሪክ አዘጋገብ የተለየ ያደርገዋል፡፡

የፕሮፌሰር መስፍንን መክሸፍ ልዩ የሚያደርገው፣ በዋናነት በእኒህ እጅግ በኢትዮጵያዊነታቸው በሚኮሩ፣ ሀገሪቷ በረጅሙ ታሪኳ ስለነበራት ጥንታዊ ሥልጣኔና ገናናነት ፈፅሞ ጥያቄ በማያነሱ ሰው መነሳቱ ይመስለኛል። በእርግጥ ባለፉት ሃያና ሰላሳ ዓመታት የብሄራዊ ጭቆና እና ቅኝ ግዛት ሀታትን/Thesis/ የሚከተሉ ፀሃፍት፣ የኢትዮጵያን ታሪክ አስመልክቶ የተለያዩ አከራካሪ እይታዎችንና ትንተናዎችን ማቅረባቸው ይታወቃል፡፡ ይህም ለተለመደው የኢትዮጵያ ታሪክ እይታና አተራረክ እንግዳ የነበረ መሆኑ የሚታወስ ነው፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን እስካሁን የታሪክ ንፍቀ-ክበቡን በበላይነት ተቆጣጥረውት የቆዩት የኢትዮጵያን ታሪካዊ ልዕልናና ጥንታዊ ገናና ስፍራ የሚያወሱ - የአክሱም፣ የዛግዌ፣ የጎንደር፣ የሀረር፣ ወዘተ ሥልጣኔዎችን የሚዘክሩና የሀገሪቱ የተዋሃደች አገረ-መንግስትነት የሚያስረግጡ ጥናቶችና ፅሑፎች መሆናቸው ይታወቃል፡፡ በረዥሙ ታሪካችን ስላሳለፍናቸው ክስረቶች፣ ውድቀቶች፣ መነሳቶች፣ ሥልጣኔዎች፣ እመርታዎች/ከፍታዎች፣ ያመለጡ ዕድሎችና ያልተሳኩ ሙከራዎች እንዲሁም ጠለቅ ያሉና ሀገራዊ እሴትን፣ ማህበረሰባዊ ስነልቦናችንን፣ የሞራል መሰረቶቻችንን፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ስርዓተ-ምህዳራችንን እና ሌሎች ቁልፍ የህልውና መሠረቶችን፤ በአጠቃላይ በእኛነታችን ዙሪያ እዚህ ግባ የሚባል ጥናት አልተደረገም፡፡ ፕሮፌሰሩ ላለፉት አያሌ መቶ አመታት በዝግታ ወይም ባለችበት እየረገጠች ነው በሚሏት ሀገራቸው ላይ ያካሄዱት የሰላ ትችት፣ ሀገርንና እራሳቸውን ነፃ የማውጣት ተልዕኮ ነው፡፡

ይህ ሙከራቸውም እንደ ቀላል የሚታይ አይደለም፡፡ መነሳት ያለበት ሌላው ጉዳይ ፕሮፌሰሩ “እንዴት ወደ ኋላ ቀረን?”፤ “ፊት እንዳልነበርን እንዴት ከመጨረሻዎቹ የመጀመሪያዎቹ ሆንን?” የሚለውን በሁሉም ኢትዮጵያዊ አዕምሮ ውስጥ የሚመላለስ የዕለት ተዕለት ጥያቄያዊ እውነታ ወደ አደባባይ ያወጡበት መሆኑ ጭምር ነው፡፡ በእርግጥ መፅሀፉ ካሉበት የትኩረት መስክ እና የዕይታ ነጥቦች፣ ፅንሰ-ሃሳባዊ ትንተናና ኃልዮቶች፣ እንዲሁም ርዕሱ ካሸከመው ዕዳ አኳያ ከተመዘነ፣ መፅሃፉ አንባቢ የሚጠብቀውን ያህል የረቀቁና የበሰሉ ሃሳቦችን በተብራራና በተሟላ መልኩ ማቅረቡን እጠራጠራለሁ፡፡ ነገር ግን ይሄ በምንም መመዘኛ የፕሮፌሰሩን መፅሐፍ ከሽፏል ሊያሰኝ አይችልም፡፡ አንድ ነገር ከሸፈ ስንል ታሪካዊ ሂደትን፣ መንስኤን፣ ውጤትንና አጠቃላይ የጊዜ እንዲሁም ሌሎች በርካታ ሳይንሳዊ ሁናቴዎችንና ዳራዎችን ከግንዛቤ ማስገባት ይገባል፡፡

የፕሮፌሰር የታሪክ ፍልስፍና እንዲህ አይነት የታሪክ መፅሃፍ፤ ፀሃፊው የሥልጣኔ፣ የባህል እና የዘመናዊነትን እንዲሁም የማህበረሰብ፣ የለውጥንና ዕድገትን ፅንሰ-ሃሳቦች እና ሀሪሶት እንዴት እንደሚገነዘብ የምናይበት መነፅር ነው፡፡ ከዚህ የታሪክ አተያይ ነው የፅሁፉን አጠቃላይ ይዘትና መንፈስ መመዘን እንዲሁም ፀሃፊው ተሳክቶለታል አልተሳካለትም የሚለውን መፈተሽ ያለብን፡፡ በታሪክ ጥናት ሁለት ዋና ዋና እይታዎች አሉ - የዑደት እና የእድገት ኃልዮቶች። ከዚህ አንፃር ሲታይ ፕሮፌሰር መስፍን ታሪክን የሚመለከቱት ወጥነት ያለው፣ ወደፊት የሚጓዙበት እና ወደላይ የሚያስወጣ የለውጥ መሰላል አድርገው ነው፡፡ ይህ የታሪክ አተያይ ቀጥተኛ የሚባለው/linear theory/ ሲሆን ሁልጊዜም ታሪክ በአዳዲስ ክስተቶችና ሁነቶች የተሞላ መሆኑንና በማያቋርጥ ለውጥ ውስጥ መገኘትን የሚያሳይ ነው፡፡ የዚህ አስተሳሰብ አራማጆች፤“ታሪክ ሁልጊዜም በተሻለ ቦታና መደላድል ላይ መገኘት አለበት” ብለው ያምናሉ፡፡ ፕሮፌሰር መስፍን በፅሁፋቸው፤ “ታሪክ አብዛኛውን ጊዜ ከታችኛው ደረጃ ወደላይኛው ደረጃ የሚያደርስ፣ ከተጎሳቆለ ኑሮ የሚያወጣውን ጉዞ የሚያመለክት የእድገት ጎዳና ሆኖ ይታያል።

አንዳንድ ጊዜ ግን አንዳንድ ሥልጣኔዎች ቶሎ ያብቡና ሳያፈሩ ቶሎ ይደርቃሉ፤ ደርቀው አይቀሩም፤ ተፈጥሮ ቆሞ መቅረትን አይደግፍም፤ ለውጥ ግዴታ ነው፤ወደተሻለ ደረጃ ካልተለወጡ ወደባሰ ደረጃ መውረዱ የማይቀር ነው፣ ወይም በሌላ አነጋገር ካላደጉና ካልተሻሻሉ መሻገትና መበስበስ፣ በስብሶ መፈራረስ ግዴታ ነው።” /ገፅ-1/ ይላሉ፡፡ ከምዕራፍ ሁለት እስከ አምስት ያሉት ክፍሎች፤ የታሪክ አተያይ፣ህብረተሰባዊ ፋይዳ፣የአጠናን ዘዴ እና የምሁራን ሚናን በንድፈሃሳቦች በማስደገፍ የሰላ ትችት የሚያቀርቡበት ነው፡፡ የፕሮፌሰር መስፍን የመክሸፍ ትርክት የሚጠነሰሰውም እዚሁ የታሪክ አተያይ ክፍል ላይ ነው፡፡ የዚህ ወጥ የታሪክ ምልከታ ሃልዮት ወይም ንድፈ ሃሳብ ይበልጥ ጎልቶ የሚታየው ስለታሪክ ምንነት በሚያብራሩበት ምዕራፍ አንድ ላይ መሆኑን መመልከት ይቻላል “ታሪክ የሕዝብ፣ የተከታታይ ትውልዶች ሥራ ነው፤ ኑሮ ነው፤ ትግል ነው፤ ተጋድሎ ነው፤ --- የቀደመው ትውልድ ኅብረቱን፤ ንብረቱንና ህይወቱን፤ በአጠቃላይ የአብሮ መኖር ህልውናውን አረጋግጦ ለሚቀጥለው ትውልድ ያስተላለፈውንና ያስተላለፈበትን ሁኔታ የሚገልፅ ቅርስ ነው።” ለእርሳቸው ታሪክ በትውልዶች ቅብብሎሽ የኋለኛው የእራሱን አክሎ የሚጓዝበት ሰንሰለታማ መንገድ/ጉዞ ነው፡፡

ይህ ነው የፕሮፌሰርን የታሪክ አተያይ ወጥ/linear/ ከተሰኘው የታሪክና ስልጣኔ ንድፈ-ሃሳብ ጎራ የሚያስመድበው፡፡ እንደ ፕሮፌሰር ስለስልጣኔ መውደቅ ያጠኑ ምሁራንና የታሪክ ፀሀፊዎች የተጠቀሙት ንድፈ-ሃሳብ ደግሞ የዑደት ኃልዮትን/cyclical theory/ ነው፡፡ ለምን ቢሉ የሥልጣኔዎች አነሳስ፣ እድገትና ውድቀት ተመሳሳይነትና ቁርኝት ስላለው ነው፡፡ ታሪክ ራሱን ይደግማል እንዲሉ፡፡ መክሸፍ እና ህልውና ፕሮፌሰር በመፅሃፋቸው እንዳሰፈሩት፣ ስለበርካታ ሥልጣኔዎች ውድቀት እና ህልፈት አያሌ መፃሕፍት እና ጥናቶች ተፅፈዋል፡፡ ኤድዋርድ ጊበን፤ የሮም ሥልጣኔ ውድቀትን አስመልክቶ የፃፈው /the decline and fall of roman empire/፣ ኤድዋርድ ሽፔንግለር ከሬናሳንስ በኋላ የተስተዋለውን የምዕራቡ ዓለም የባህልና የፍልስፍና አስተምህሮቶች ዝቅጠትን አስመልክቶ የፃፈው /the decline of the west/ እና አርኖልድ ቶይንቢ፣ የአለም የሥልጣኔ ታሪክ ጥናትን በተመለከተ የፃፈው /the study of history/ በዋነኛነት ይጠቀሳሉ፡፡

ከቅርብ ሥራዎች ደግሞ ጃክዊስ ባሩዝ የምዕራቡን ባህልና እሴቶች መሸርሸር አስመልክቶ የፃፈው /From Down to Decadence 1500 to the Present: 500 Years of Western Cultural Life/ (2000) ተጠቃሽ ነው፡፡ የሃያኛው ክፍለ ዘመን ልዕለ ኃያሏ አሜሪካ የሃይል ሚዛን ማሽቆልቆል እና ወደ ምስራቁ ዓለም /እስያ/ በተለይ ወደ ቻይና እና ወደ ሌሎች አዳዲስ አገራት መሸጋገር አሁን የአካዳሚውንና የሚዲያውን ምህዳር በስፋት የተቆጣጠረ ጉዳይ ሆኗል፡፡ የታሪክ ሊቁ አርኖልድ ቶይንቢም እንደሚለው፣ በታሪክ ከምናውቃቸው ሃያ ሁለት ሥልጣኔዎች መካከል አስራ ዘጠኙ የወደቁት አሁን አሜሪካ የደረሰችበት የሞራል ዝቅጠት ደረጃ ላይ በደረሱ ወቅት ነው፡፡ በአጠቃላይ ላለፉት አምስት መቶ አመታት ገደማ የአለም ሥልጣኔ ምህዋርን በበላይነት/ በኃያልነት ሲዘውር የቆየው የምዕራቡ ዓለም ማሽቆልቆል እና ውድቀት ምሁራኑንና ፖሊሲ አውጪዎቹን ከፍ ባለ ትካዜ ውስጥ እንዲገቡና አብዝተው ስለመውጫ መንገዶች እንዲያስቡ ያደረጋቸው የታሪክ ምዕራፍ ሆኗል፡፡

በዘመናዊው የታሪክና የሥልጣኔ ጥናት መክሸፍ/፣ ውድቀት/fall/፣ ምክነት /decadence/ ንቅዘት/decay/፣ ክስረት /bUNCRUPTCY/፣ ዝቅጠት/degeneration/፣ ማሽቆልቆል/decline/ ወዘተ በአብዛኛው ለአንድ ማህበረሰብ የሞራልና የስነ-ምግባር እሴቶች መላሸቅ፣ የሥልጣኔ እና የአዳዲስ ሃሳቦች እንዲሁም የፈጠራ መጥፋት፣ የሀሳብ ተዋስዖ እና የምርምር ውጤቶች መዳከም፣ የፖለቲካ ስርዓት ሕዝባዊ ወገንተኝነትና ተጠያቂነትን በተለይ የነፃነት እጦትን፣ የፍትህ አለመኖርንና የህግ የበላይነት መሸርሸርን፣ የባህል አለመዳበርንና አለመጎልመስን፣ የኢኮኖሚ ለውጥና አጠቃላይ ብልፅግናን ብሎም ተጠቃሚነት አለመኖርን፣ የስነ-ጥበብና ኪናዊ ሥራዎች መፋዘዝን፣ የማህበራዊ ቀውሶች መበራከትን፣ የማህበረሰብ የስነ-ልቦና ዝቅጠትንና ተስፋ መቁረጥን እና ደስተኛ አለመሆንን፣ የጋራ ማህበረሰባዊ ራዕይና ግብ ያለመተለምንና የመፋዘዝ አባዜን፣ በአጠቃላይ በማያቋርጥ አዎንታዊ የለውጥ እና የዕድገት ሂደት ውስጥ አለመገኘትን የሚያመላክቱ ፅንሰ-ሃሳባዊ ቃላቶች ናቸው፡፡

አንድ ማህበረሰብ በታሪክ ከነበረው ስፍራ ጋር ሲመዘን አሁን ያለበት ቦታ እና መሆን በሚገባው መሀል የጎላ ልዩነት ሲፈጠር እንዲሁም ጉዞው ያንን እውን እንደማያደርግ የሚያመላክት ሲሆን እነዚህ ፅንሰ-ሃሳባዊ ቃላቶች ጥቅም ላይ ይውላሉ፡፡ ምንም እንኳን ከፅንሰ-ሃሳባዊ ማዕቀፍና አተያይ አኳያ በቃላቱ መሐል የሂደት እና የደረጃ ልዩነት ቢኖርም የሚያመላክቱት ተመሳሳይነት ያለው ነባራዊ ወይም መፃዒ ሁኔታን ነው፡፡ ፕሮፌሰር መስፍን ፤ መክሸፍ የሚለውን ቃል የመረጡት እነዚህን ከላይ የተጠቀሱትን አላባዎች በአንድ ላይ አሰናስሎ ሊይዝ የሚችል ቃል ከመፈለግ አኳያና በህብረተሰቡ ውስጥ ሊፈጥር የሚችለውን አንድምታ ከግንዛቤ በማስገባት ይመስላል፡፡ ፕርፌሰር መክሸፍን ሲያብራሩ “መክሸፍ የምለው አንድ የተጀመረ ነገር ሳይጠናቀቅ ወይም ሳይሳካ እንቅፋት ገጥሞት መቀጠል ሳይችል፣ ዓላማው ሲደናቀፍና በፊት ከነበረበት ምንም ያህል ሳይራመድ መቅረቱን ነው፣ የእድገት፣ የመሻሻል፣ የመለወጥ ጉዞ መቋረጥን የሚያመላክት ነው፡፡”ይላሉ፡፡ ከዚህ የፕሮፌሰር ትርጓሜ የምንረዳው መክሸፍ ሁለት ሁኔታዎችን የሚያካትት መሆኑን ነው - አንደኛው የነገሮች ተጀምሮ አለመጠናቀቅንና ባሉበት መቅረትን ሲሆን ይህም ከጅማሮ የማይዘሉ ነገር ግን መጀመራቸው ብቻ የሚወሱ የታሪክ ኩነቶችን የሚያስረዳ ነው፡፡ በዚህ ውስጥ የመገታትና የመቋረጥ ድምፀት ይስተዋላል፡፡ ሁለተኛው የባሰውኑ ቁልቁል መውረድንና ከነበረው ወደ ኋላ መቅረትን/የኋሊት ጉዞን/ የሚያመላክት ነው፡፡

በአጠቃላይ የዕድገትና የለውጥ መገታትን ብሎም በትውልዶች መሀል ቅብብል አለመኖር ወይም ሁልጊዜ ከዜሮ እንደ አዲስ መጀመርን ፤ ለምሳሌ ተቋማትን ያለመገንባት፣ የባህል ለውጥና የህብረተሰብ ሽግግር አለማድረግ፣ የኢኮኖሚያዊ ስርዓተ-ምህዳራችን አለመዘመን፣ የፖለቲካ ስርዓታችን በህዝብ ነፃ ፈቃድ ላይ የተመሰረተ በወል ህግ የሚተዳደርበት እና መሠረታዊ ነፃነቶችን የሚጠብቅ ለማድረግ አለመቻላችን ብሎም የህዝብ ሉአላዊነት ልዕልና አለማግኘት እጅግ መሠረታዊ ነጥቦች ናቸው፡፡ እርሻ ቀድመው ከጀመሩ ህዝቦች አንዱ የሆነ ህዝብ እንዴት እስካሁን በቴክኖሎጂ የታገዙ የተሻሻሉ የአመራረት ሂደቶችን እና ኢኮኖሚያዊ ስርዓትን መፍጠር አቃተው? የሚል ጥያቄ ለዚህ እንደ ማስረጃ ይቀርባል፡፡ ፕሮፌሰሩ በገጽ 27 ላይ “….እኔ ከመክሸፍ ሌላ የነበረ እና ያለ አይታየኝም…” ብለው አስረግጠው ይናገራሉ፡፡ ከፍም ሲል መክሸፍ ባህል መሆኑን ለማስገንዘብ ይሞግታሉ፡፡ መክሸፍ ባህል መሆኑን ለማሳየትም ከላይ ከተጠቀሱት አላባዎች ማሳያ ናቸው የሚሏቸውንና በታሪክ የከሸፉትን ይዘረዝራሉ፡፡

ለፕሮፌሰር መስፍን ያልከሸፈ ሃይማኖት፣ ያልከሸፈ የፖለቲካ ስብዕና ወዘተ-- የለም፡፡ እዚህ ላይ የተወሰኑቱ ከሸፉ ለማለት የማያስደፍሩ ይልቁንም በታሪክ ላደረሱት ጥፋትና መክሸፍን ባህል ስለመደረጉ እንደማስረጃ ሊቀርቡ ሲገባ የመክሸፍ ማሳያዎች ተደርገው መቅረባቸው የፕሮፌሰሩን የክሽፈት ሚዛን ጥያቄ ውስጥ ይከተዋል፡፡ ለምሳሌ መንግስቱ ከሸፈ ከማለት ይልቅ አብዮቱ ከሽፏል ወይም የስድሳዎቹ ትውልድ ከሽፏል ቢባል የተሻለ ሃሳባቸውን የሚያጠናክር ሃልዮት ሊሆን በቻለ ነበር። ይህም ቢሆን ለውስንነቶች የተጋለጠ ነው። ዘለቅ ሲል ፕሮፌሰሩ በታሪካችን ውስጥ ጨርሰው የከሸፉ ያሏቸውን ተቋማትና ማህበሮች ሲዘረዝሩም - የሐረር ጦር አካዳሚ፣ የኢትዮጵያ የባሕር ኃይል ኮሌጅ፣ የኢትዮጵያ አየር ኃይል፣ የኢትዮጵያ የምድር ባቡር ሲሆኑ በማህበራት በኩል የኢትዮጵያ ሠራተኞች ማህበርንና የኢትዮጵያ መምህራን ማህበርን በማስረጃነት ይጠቅሳሉ፡፡ ለፕሮፌሰር መስፍን ያልከሸፈ አንድ ነገር ብቻ ያለ ይመስላል/ገፅ10/፡፡ ይኸውም ትውልዶች ለዚህች ሀገር ነፃነትና ሉአላዊነት መከበር ያለአንዳች ስስት እራሳቸውን መስጠታቸው ነው፡፡ ነገር ግን እዚህ ጋ ፕሮፌሰሩ ሳያነሱ የቀሩት አንድ ጉልህ ቁምነገር አለ፡፡

ይኸውም ከሉአላዊነትና ከግዛት ነፃነት ከፍ ስላለውና የሀገር ህልውና መሠረት ስለሆነው፣ እንዲሁም ከትውልዶች በላይ ስለሚሻገረው - የተሻለችና የበለፀገች ሀገርን ለቀጣዩ ትውልድ ለማውረስ አለመስራታቸውን የተመለከተ ሲሆን ስለዚህ ጉዳይ ፕሮፌሰሩ ያለፈውን ትውልድ አልሞገቱም፡፡ ለእርሳቸው፣ የቀድሞው ትውልድ ተልዕኮ ከአርበኝነት አኳያ ብቻ የታየ ይመስላል። ብቸኛው በትውልዶች ቅብብል የቀጠለ/ህልው ያገኘም ይሄ ነው፡፡ እዚህ ጋ የህልውና ትርጉማቸው ጭምር ከታሪካዊው የሉዓላዊነት ጥያቄ አኳያ ብቻ የሚመነዘር ይመስላል/ገፅ11/፡፡ በዚህም አተያያቸው ኢትዮጵያን የቀደመ ሥልጣኔዋን ሰርታ አብቅታ መሻሻልና መለወጥ ያላስፈለጋት፤ በልጆቿ የምትጠበቅ ሀገር አስመስለው አቅርበዋታል፡፡ ይህም የክሽፈት ምልከታቸውን እጅግ ያሳሳው ከመሆኑም ባሻገር፣ በታሪካዊ ዳራዎች ላይ ጠለቅ ያለ ምርምር አለማቅረባቸውን የሚያስረግጥ ነው፡፡ ሆኖም ይህንን አተያያቸውን ስለህልውና በሚያወሱበት መደምደሚያ ላይ በተሻለ አቀራረብ ለመሞገት ችለዋል፡፡ በፕሮፌሰር እይታ ትልቁ የመክሸፍ ምክንያት ባህል ነው፡፡ ባህላችን የቆመበትን የጓሮ ፍልስፍና ሁሉ ብንመረምረው ለእድገትና ለመሻሻል የሚመች አይደለም፤ የእድገትና የመሻሻል እንቅፋቶች፤ አእምሮ ውስጥ ተሰርገው ሰው የተሻለ ነገር እንዳይመኝ የሚያደርጉ ስነ-ልቡናዊ ህጸጾች ናቸው የሚሉት ፕሮፌሰሩ፤ለዚህም የአነጋገር ፈሊጦችን እንደማስረጃ ያቀርባሉ፡፡

ከዚሁ ጋር አያይዘው በየዘመኑ የሚከሰተውን አዲስ ችግር እያጠኑ፣ በየወቅቱ የሚመጣውን አዲስ ስልት በመማር አዳዲስ ሃሳቦችን ለማመንጨት ባለመቻሉ፣ አዲስ የእድገት ጎዳና ለመጥረግ አለመቻሉን ይገልፃሉ። ፕሮፌሰር ምንም እንኳ እንደእነ ዘርዓ ያዕቆብ ላለው ሀገር በቀል ሃሳቦች፣ የታሪክ ጥናት እና ባህል ልዩ ስፍራ ቢሰጡም፣ ይህ እምነታቸው ዘመናዊ ትምህርት በቀሰመው አውሮፓዊው አእምሯቸው ሲመዘን፣ መሻሻልና መለወጥን እንዲሁም ከምዕራቡ ዓለም የመማርን አስፈላጊነት አበክረው የሚሰብኩ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ ለእርሳቸው ዝመና እና ዘመናዊነት ከአኩሪ ባህሎች ጋር ተቆራኝቶ እና ተስማምቶ የሚሄድ የሥልጣኔ ዘዬ ነው፡፡ ይሄም የተለመደውን የዝመና እና የባህል ተቃርኖ ለማለዘብ ያሰቡ ያስመስላቸዋል፡፡ ሌላው መነሳት ያለበት ፕሮፌሰር መስፍን የባህል ተቺ/cultural CRITIC/ መሆናቸው ነው፡፡ በ2003 ዓ.ም ባሳተሙት “ሥልጣን ባህልና አገዛዝ - ፖለቲካና ምርጫ” በሚለው መፅሃፋቸው እንዲሁም በአሁኑም ሥራቸው ጭምር ይሄ የባህል ተቺነታቸው ጎልቶ ይታያል፡፡ የባህል ተቺነታቸው ብቻ ግን አይደለም፡፡ የባህል ጨለምተኝነት ተዋስዖ/cultural pessimism/ በተወሰነ መልኩ የሚስተዋልባቸውም ይመስላል፡፡

ለዚህ በቂ አመክንዮ ቢኖራቸውም አሁን ያለው ባህል በምን አይነት የታሪክና የሁነቶች ተቃርኖና አንብሮ እንደተፈጠረ እንዲሁም የሌሎች ማህበራዊ ክስተቶች ነፀብራቅ መሆኑን በቅጡ መርምረው አላሳዩም፡፡ ይህም በተለምዶ “ባህላችን ነው ኋላ ያስቀረን” ከሚለው ትርክት እንዳይወጡ እና የተጠና ምልከታ እንዳያቀርቡ አግዷቸዋል። ባህል የማህበራዊ ስሪቶች ውጤት/social constructivism/ ጭምር መሆኑን አለመቀበላቸው ሌላው የዚሁ ፈተና አካል ነው፡፡ እንዴት ይህን ማህበራዊ ስሪት በሂደት አዳበርን? በምርጫችንና በታሪክ በተጋፈጥናቸው ፈተናዎችና ተግዳሮቶች ብሎም ተቃርኖዎች መሆን አለመሆኑን ለመረዳት በቂ ጥረት ያደረጉ አይመስልም፡፡ ፕሮፌሰር በብዙ መልኩ በኢትዮጵያዊው ባህል የሚኮሩ ቢሆንም ለዘመናዊው ለውጥ እና አኗኗር እጅግ ጎታች መሆኑንም ልብ እንዳሉ መገንዘብ አያዳግትም፡፡ ነገር ግን ሃሳቡ አእምሮና መንፈስን በሚሞግት መልኩ አይደለም የቀረበው፡፡ ሌላው እንደ አንድ ችግር መጠቀስ ያለበት ደግሞ የፕሮፌሰር መስፍን የአፃፃፍ ዘዬ እና ነገሮችን እንደወረዱ የማቅረብ ስልታቸው የፈጠረው ተግዳሮት ነው፡፡ በፕሮፌሰሩ መፅሃፍ ጥሩ እይታ የተቸረው ሌላው ርዕሰ ጉዳይ ዘመናዊነት/ዝመና /modernism/ ነው፡፡ ፕሮፌሰሩ በአመክንዮ የውጭ ባህልና ምዕራባዊ ሥልጣኔን መቀበል ተገቢ ነው የሚል ቃና ይስተዋልባቸዋል፡፡ ይህም ሲሆን ግን ከአጓጉል መጤ ባህሎች እራስን በመጠበቅና ማንነትን ጠይቆ በማግኘት እንዲሁም የወደፊቱን ህልውና በሚወስን ሁኔታ ላይ የተመረኮዘ ያደርጉታል፡፡

ፕሮፌሰሩ የባህልና ዘመናዊነት ተቃርኖን በማለዘብ አስታራቂ ሀገራዊ ቀመር እንደሚያስፈልግ፤ ለሀገር በቀሉ አስተሳሰብና ኢትዮጵያዊ ዕውቀትም ተገቢውን ቦታ መስጠት እንደሚገባ ያሳዩበት መልክ፣ አውሮፓዊውን/አሜሪካዊውን መስፍን በኢትዮጵያዊው መነፅር ለማየት ያስችለናል፡፡ ለዚህም ነው ለታሪክ ጥናትና ለእውነት ተገቢው ዋጋ እንዲሰጥ የሚወተውቱት፡፡ ለዚህም ነው ዘመናዊው አእምሯቸው ከእውቀት ስለሚገኝ እውነት፣ ስለባህል መለወጥ፣ ስለመሠረታዊ ነፃነቶች መጠበቅና ሁሉን አሳታፊ፣ የሕዝብ ሉዓላዊነትና ፍትህ የሰፈነበት ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ስለመገንባት በአጠቃላይ ሥልጣንን ስለመግራት የሚጨነቀው፡፡ ይሄ ደግሞ ዘመናዊነትን በኢትዮጵያዊነት ውስጥ የመፍጠር እሳቤ ውጤት ነው፡፡ ምዕራባውያን ስለ ባህላቸውና ስለሥልጣኔያቸው እጣፈንታ መጨነቅና መጠበብ በያዙበት ወቅት፣ እንደኛ ላለችው በውጣ ውረድና እራስን መልሶ በማግኘት ፈተና ውስጥ ላለች አገር፣ ይሄ የሚበዛ ጥያቄ አይመስለኝም፡፡ ከዚሁ ጋር የሚያያዘው ሌላው የመክሸፍ መንስኤ ሃይማኖት እና የእውነት መረጋገጥ ሳይሆን መገለጥ ነው፡፡

ለእርሳቸው እውነት ሁለት መሠረቶች አሉት፤ ከእምነትና ከእውቀት፡፡ እንደ እርሳቸው፣ ከእምነት የሚፈልቅ እውነት አያከራክርም፤ ለሙግትና ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም፡፡ ይህንንም የሚያጠናክር ሌላም ምንጭ አለው፤ ሥልጣን፡፡ ኢትዮጵያ የተገለጠ እውነት ሀገር እንደመሆኗ ለጥያቄና ለክርክር ክፍት ያልሆነ ማህበረሰብና አስተሳሰብ የነገሰባት ነች ይላሉ። ለሥልጣኔዋ ወደ ኋላ መቅረትና ማሽቆልቆልም ሰበቡ የእውቀት ጥበብ ተቋዳሽ አለመሆናችን እንደሆነ አፅንዖት ሰጥተው ይሞግታሉ። ይህንም ሲያጠናክሩ “በረጅሙ ታሪካችን ያልደረስንበትና ያቃተን አንዱ ዋና ነገር በተረጋገጠ እውነት እየተመራን ልማትን፣ እድገትንና ብልፅግናን ለማምጣት አለመቻላችን ነው” ይላሉ፡፡ እዚህ ጋ ግን ልብ ያላሉት አብይ ጉዳይ ያለ ይመስለኛል። ይኸውም ከእምነት የሚመነጭን እውነት የመጠየቁና የመሞገቱ እድል በአንፃራዊነት ጠባብ ቢሆንም፣ መንፈሳዊ እውቀትንና አስተምህሮውን በመመርመር፣በእውቀት ላይ የተመሰረተ እምነት ማካሄድ እንደሚቻል አለማሳየታቸው ነው፡፡ እንደ እኛ ባለ ማህበረሰብ ውስጥ የባህልና የእምነት ሚናን ለመነጣጠል እጅግ አዳጋች ነው፡፡

በኢትዮጵያ ከእምነት ባልተናነሰ እንደውም በላቀ መልኩ ባህል፣ ወግና ልማድ የእውነት ምንጭ ሆነው ይስተዋላል። ባህላችንም የእምነታችን ምንጭ፤ እምነታችንም የባህላችን ምንጭ መሆኑን ዘንግተውታል፡፡ የዚህ ፅሑፍ አቅራቢም እንደሚስማማው፤ ለእርሳቸው እውነት ፍትህ ናት፣ ልማት ናት፣ ዴሞክራሲ ናት፣ ታሪክ ናት ወዘተ፡፡ ይህን ባህልና አስተሳሰብ ለመፍጠር የሚቀድመው በሰው ልጅ ላይ ትኩረት አድርጎ መስራት ነው፡፡ የቀደመው ሥልጣኔያችን ዋነኛ ጉድለት ስለ ዕውቀትና አብርኆት፣ ስለአመክንዮና ኃልዮት በአጠቃላይ ሰው ላይ ይህ ነው የሚባል ስራ አለመስራታችን እንዲሁም ታላላቅ ሃሳቦችን/ፍልስፍናዎችን አለማንሳታችን መሆኑን ፕሮፌሰሩ በጥልቀት አልተመለከቱም፡፡ ይህ ደግሞ እንዴት ያ የጥንቱን ሥልጣኔ ያፈራች ሀገር፣ ሰውን መሠረት ያደረገ ዘመናዊ ሥልጣኔ መፍጠር አቃታት? የሚለውን የመፅሐፋቸውን መሠረታዊ ጥያቄ በውል እንዳይዳስሱና እንዳይተነትኑ አግዷቸዋል፡፡ በዚህ ፅሑፍ ላይም ለመግለፅ እንደተሞከረው የአውሮፓ ሥልጣኔ መሠረቱ ሰው ነው፡፡ የጥንታዊት ኢትዮጵያ ሥልጣኔ መሠረቱ ደግሞ ሃይማኖት ነው፡፡ ሁለተኛውም መሠረታዊ ጥያቄ የሚሆነው ይህ ሐይማኖታዊ ሥልጣኔ፣ ዘመናዊው ሰውን ማዕከል ወዳደረገው ሥልጣኔ እንዴት መሸጋገር አቃተው? የሚለው ነው፡፡

እንደ ምዕራቡ የአስተሳሰብና የባህል፣ የተሃድሶና የአብርኆት አብዮቶችን ባለማካሄዳችን ይሆን? እንግሊዛዊው የታሪክ ሊቅ አርኖልድ ቶይንቢ The Study of History በሚለው እና የአለም ሥልጣኔዎችን አነሳስና ፍፃሜን በሚያትተው ዘመን ተሻጋሪው መፅሐፉ፣ ሥልጣኔዎችን በሃይማኖት መነሾ በስምንት የከፈላቸው ሲሆን ጥንታዊውን የኢትዮጵያ ሥልጣኔም “የኦርቶዶክስ ክርስቲያን ሥልጣኔ” በሚለው ክፍል ውስጥ መድቦታል። ፕሮፌሰር መስፍንም ታላላቅ ሥልጣኔዎችን አስመልክቶ፣ በውጭ ፀሐፍት የተፃፉ መፃህፍትን በተለይ የአርኖልድ ቶይንቢን ማየታቸውን መገንዘብ ይቻላል፡፡ በ2003 ዓ.ም በታተመው “ሥልጣን ባህልና አገዛዝ” በሚለው ሥራቸው በገፅ 83 አርኖልድ ቶይንቢ፣ ጃፓንና ኢትዮጵያን ያነፃፀረበትን አተያይ በምሳሌነት ማቅረባቸውን ልብ ይሏል፡፡ ምንም እንኳ በዘመናዊው ዓለም ከእውቀትና ምክንያት ከፍም ሲል የሰውን ልጅ መሠረት ያደረገ ሥልጣኔ መፍጠር እጅግ የማይተካ የሥልጣኔዎች መሠረት መሆን እንዳለበት ቢታመንም፣ ጥንታዊ ሥልጣኔዎች ከሃይማኖታዊ አስተምህሮም የፈለቁ መሆናቸውን መረዳት ይገባል፡፡

በዘመናዊው የእውቀት ዓለምም የፍልስፍና እና ሃይማኖት ግጭት ወይም ተቃርኖ የሚጠቀስ ቢሆንም የሁለቱ ተስማሚነትና ተደጋጋፊነትም አብሮ መታየት ያለበት ጉዳይ ነው። በኢትዮጵያም ለዓለማዊውም ሆነ ለመንፈሳዊው ዓለም ችግሮች፣ ሃይማኖታዊ አስተምህሮዎች መነሣታቸው ተገቢ ነው፡፡ ከሃይማኖት ስለዓለምና ስለሕይወት ብዙ እውቀቶች መገኘታቸውን መረዳት ይቻላል፡፡ ሌላው ደግሞ የባህልን የዕውቀት አበርክቶ/epistemic culture/ ከግንዛቤ ያላስገባ እና እውቀት ከአንድ ማህበረሰብ ማህበራዊና ባህላዊ ሃሪሶት እና ስሪት ሊመነጭ የሚችልበትን ዘመናዊውን የዕውቀት አረዳድ ኃልዮት ከግምት ያላስገባ መሆኑ ነው፡፡ ነገር ግን ፕሮፌሰር ባነሷቸው መልኩ የቀረቡት የሃይማኖት/እምነት እና የእውነት ሙግት ከማህበረሰባዊ አንብሮ አንፃር ተገቢ ትችት መሆኑ የሚነግረን ትልቅ እውነት አለው፡፡ ፕሮፌሰሩ እንደሚያስረዱት፤ዋናው የክሽፈት መዘውር የተያዘው ሥልጣንን ለመግራት ባለመቻላችን ነው፡፡ በቀደሙት ሥራዎቻቸውም ለዚህ ማሳያ ይመስላል “አገዛዝ” የሚለውን ቃል በተደጋጋሚ የሚጠቀሙት፡፡ ሕግና ስርዓት እንዲሁም አስተዳደር ለማህበረሰብ ዕድገት ቁልፍ መሆናቸውን ያስረዳሉ፡፡

“ሥልጣን” ይላሉ ፕሮፌሰር “የአንድ ማህበረሰብ ነፍስ ድልድል ነው ለማለት ይቻላል፤ ሥልጣን ሁሉ በአንድ ወይም በጥቂቶች ሰዎች እጅ ተቋጥሮ ሌላው ሁሉ በአንድ ወይም በጥቂቶች ሰዎች ኃይል ብቻ የሚሽከረከር በድን ከሆነ ማኅበረሰቡ ነፍስ የሌለው አካል ነው” ሲሉ ይሞግታሉ፡፡ በዚህም ፕሮፌሰር፤ የምዕራቡ በወል የሚተዳደር የውክልና እና የሕዝብ ሉዓላዊነት ላይ የተቋቋመ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት የመፍጠር እና መሠረታዊ ነፃነቶችና መብቶችን መጠበቅ አስፈላጊነትን አበክረው ይተነትናሉ፡፡ ይህም የሰው ልጅ የነገሮች ሁሉ መሠረት፤ የህላዌ ማዕከል መሆኑን ለማሳየት አጠቃላይ ማህበራዊ አረዳድ ብሎም ባህል በሀገሪቱ መፍጠርን ይጠይቃል፡፡ እንዴት ይህን ባህልና ስርዓት እንፍጠር የሚለው ሌላው መሠረታዊ ጥያቄ ነው፡፡ የእነዚህ መሠረታዊ ጥያቄዎች መነሳት፣ ሀገሪቱ ምን ያህል ያልተሻገረቻቸው ጭራሽም ያልጀመረቻቸው የህልውና ጥያቄዎች በርካታ መሆናቸውን ይጠቁመናል፡፡ (በዚህ ፅሑፍ አቅራቢ እምነት፣ መሠረታዊው የዘመናዊነት ኢትዮጵያ የህልውና ተግዳሮት የነፃነቶች እጦት ነው፡፡) ለዚህም ሥልጣንን መግራት እና በእውቀት ከተረጋገጠ እውነት ጋር መተዋወቅ እንዲሁም መጠየቅን፣ ሃሳብ መለዋወጥን እና የአእምሮ ብልፅግና ላይ መሠራት እንዳለበት ፕሮፌሰሩ ይሞግታሉ፡፡ ለዴሞክራሲያዊና በሕግ ለተገደበ ስርዓት አለመሥፈን ዋነኛ ማነቆ የሆነው የሀገሪቱ የፖለቲካ ባህል መሆኑንም የተረዱ ይመሥላሉ፡፡

እጅግ ዘመናዊ ህገ-መንግስትና ሌሎች ምርጥ የምዕራቡ ዓለም ህጎች ቢኖሩም፣ የሚሰሩበት ባህልና ተቋም ያው በቀድሞው ከሆነ ምንም ውልፍት ሊያደርግ የሚያስችል አይደለም፡፡ ይበልጥ ማህበራዊ ቀውስ ነው የሚያስከትለው፡፡ ፕሮፌሰር መስፍን፤ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ስርዓት ላይ እጅግ ተገቢ የሆነ ምሬት ያንፀባርቃሉ፡፡ ከአገራቸው ኋላ የመጡ አገራት ወደ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ሲሸጋገሩና ስልጣንን በሕግ ገድበው ሲቆጣጠሩ፣ ሀገራቸው ግን ሂደቱ እጅግ አድካሚና በአቀበት ቁልቁለት የተሞላ እንደሆነባት ታዝበዋል፡፡ይሄ ክሽፈት የሚጠቁመን ቁምነገር ቢኖር አንድም ከእነአካቴው አለመጀመሩን ወይም ለመጀመር አለማሰባችንን አሊያም ብልጭ ብሎ መጥፋቱን ሊሆን ይችላል፡፡ ለዚህም ፕሮፌሰሩ የሚያቀርቡት መፍትሄ የሰው ልጅ ላይ አተኩሮ በመሥራት እና ሰውን ማዕከል በማድረግ ሀገሪቷን እንደገና የመሥራት ሥራ እንደሚያስፈልግ ነው፡፡ [---] የጥንቱ ግሪካዊያን ሥልጣኔ መሠረቱ ሰው ነው፡፡ የነገሮች መጀመሪያም መጨረሻም ሰው ነው። ለዚህም ነው ምዕራባውያን እስካሁን በቀጠለው ሥልጣኔያቸው ስለሰው ልጅ የሚጨነቁትና የሚጠበቡት፡፡ የሥልጣኔው መሠረት፣ የህላዌው መልህቅ ሰውና ሰው ብቻ ነው፡፡

ምዕራባውያኑ ይህን ሰውን መሠረት ያደረገው ሥልጣኔያቸውን በሬናሳንስ እና አብርኆት እንቅስቃሴዎች መልሰው ለማግኘት ችለዋል፤የእስካሁኑ ሥልጣኔያቸውም ህላዌ ሆኖ ይገኛል፡፡ በኢትዮጵያውያን የ3ሺህ ዘመን ሥልጣኔ መቼ ነው ሰው ላይ የሰራነው? ለኢትዮጵያውያን ሰው የፈጣሪውና የአምላኩ ፍላጎት ማስፈጸሚያ ነው፡፡ በራሱ ህልውና ኖሮት የሚቆም እና ከፍ ያለ የመጠየቅ፣ የማወቅ እና የመመራመር ተሰጥኦችን ለመከጀልና ለማዳበር የተፈቀደለት አይመስልም። ለዚህም ነው የፕሮፌሰር መስፍን መፅሀፍ ፍፁም ስኬት የሚያጠራጥረኝ፡፡ መክሸፍን ለማስተዋወቅ መድፈሩ፣ ከፍም ሲል አንዳንድ ውኃ የሚያነሱ ማስረገጫዎችን ለማንሳት መቻሉ የመፅሀፉ ጥንካሬ ቢሆንም በተሟላ መልኩ የተተነተነ እና የተብራራ ጥልቅ ምልከታ የተደረገበት ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡ ከዚህ አንፃር ከታየ መፅሐፉ በህፀፆች የተሞላ ነው፡፡ እርሳቸውም በመፅሐፋቸው ሥራው የታሪክ ፀሐፊዎችና አጥኚዎች መሆኑን ጠቅሰው፤ ነገር ግን እስካሁን ስለመክሸፍ ተደፍሮ ብዕር ሊነሣ ባለመቻሉ የፈጠረባቸውን መብሰልሰል እንደጅማሮ ለማሣያነት ያቀረቡት መሆኑን አስገንዝበውናል። በፕሮፌሰር መስፍን መፅሐፍ ውስጥ እጅግ ጎልቶ የተስተጋባው ድምጸት ለውጥ ነው፡፡

ይህም የቆምንባቸውን አጠቃላይ ማህበራዊ/ባህላዊ፣ የሞራልና ስነ-ልቦናዊ፣ የእምነት፣ ፖለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ አእማዶችን በሙሉ ገንድሶ የሚጥል ስር ነቀል ለውጥ እና አብዮት የሚጠይቁ አድርጓቸዋል፡፡ በእነዚህ ሁሉን አቀፍ እና ፈርጀ ብዙ መሠረቶቻችንና አእማዶቻችን ብሎም እኛነታችን ላይ የተነሳ ብዕር በመሆኑም ይመስላል ፕሮፌሰሩን እና ሥራቸውን አብዝተን ካላቸው የፖለቲካ እምነትና አቋም አኳያ በማንፀር ልንወስድ የሚገባንን ትምህርት እንዳናጣ የምሰጋው፡፡ ገዥው ፓርቲ፤ የህዳሴውን ጅማሮ እያበሰርኩኝ ነው በሚልበት ሰዓት ላይ የቀረበ ስራ ከመሆኑ አኳያ፤ አሁን ሀገሪቷ በሁለቱ ጎራ/ወገን የምትታይበትን እና ለመፍጠር የሚያልሟትን ኢትዮጵያ አጉልቶ ለማንፀር የሚያስችለን ጉልህ ሥራ ሆኖ ሊጠቀስ ይችላል፡፡ የፕሮፌሰር መስፍን ተቃርኖዎች ዋነኛው የፕሮፌሰር ተቃርኖ የሚጀምረው ስለለውጥና ቀጣይነት/change and continuity/ ባላቸው እይታ ነው። የሚጀመሩ አዳዲስ ክስተቶች የቀደመውን በማቋረጥ ወይም በመግታት አንፃር ብቻ የማየት አዝማሚያ ያይልባቸዋል፡፡ ይህም የጥንቱ ዘመን ሥልጣኔ እና ታሪካዊ ትውፊት የፍቅር ቁርኝት/nostalgia/ አለመሆኑን ለማሳየት በሚጠበቅባቸው ደረጃ አልተጉም፡፡

ሁሉም ነገር ድሮ ቀረ የሚሉ ይመስላል። ይህም የግሪኩ ፈላስፋ ሂሲዮድ “የወርቃማ ዘመን”ን አተያይ ተጋሪ አስመስሏቸዋል። መክሸፍን የዘመናዊው ኢትዮጵያዊ ተፈጥሮአዊ መገለጫ የማድረግ አዝማሚያም በፅሁፋቸው ይታያል፡፡ ይህ ደግሞ ስለለውጥና ህልውና ለማውራት እጅግ ከፍ ያለ የማይወጡት ተቃርኖ ውስጥ ከትቷቸዋል፡፡ ለእርሳቸው አሁን ታየ የሚባለው ለውጥ የውሸትና ሕይወት የሌለው/ውስጡ ባዶ የሆነ/ አድርገው በመረዳታቸው የመጣ መሆኑን መገንዘብ ይቻላል፡፡ ይህም በቂ አመክንዮ ያለው አተያይ ውጤት ቢሆንም ችግር የሚመጣው ከመንግስታዊ/ስርዓት እይታ ብቻ የሚመነጭ ከሆነ ነው፡፡ ፕሮፌሰር ኢትዮጵያን ጥንት ተጀምራ ጥንቱኑ የተጠናቀቀች እና ከቆመችበት ፈቀቅ ማለት ያቃታት ሀገር አስመስለው ነው ያቀረቧት፡፡ ያም ቢሆን ግን ቀደም ሲል እንደጠቀስኩት በአጠቃላዩ የእኛነታችን አእማዶች ላይ ያነሱት የሰላ ትችት በመሆኑ ከግንዛቤ ውስጥ ሊገባ ይገባል፡፡

ለነገሩ ቶይንቢ እንደሚለው፤ የሥልጣኔዎች ውድቀት የሚጀምረው ያለፈ ማንነታቸውን በማምለካቸው ከሚመጣው ከልክ ያለፈ ኩራት ነው/civilizations decay due to a worship of their “former self”/፡፡ እርሳቸውም የዚሁ ሰለባ የሆኑ ይመስላል፡፡ ለዚህም “ሥልጣኔዎች እራሳቸውን ይገላሉ/ያጠፋሉ እንጂ አይገደሉም”/civilizations die from sucide, not by murder/ ለሚለው ዕውቅ የቶይንቢ ጥቅስ መክሸፍ በአቻነት የቆመ ይመስላል፡፡ መክሸፍ ባህል ነው ብለው ከተነሱ በኋላ ለዚህም የትምህርት ሚና ጉልህ መሆኑን ያወሳሉ፡፡ ቀጥሎም የዚህ የክሽፈት ባህልነት ወደ አዲሱ ትውልድ መሸጋገሩን ያረዱናል፡፡ የዚህን ትውልድ ክሽፈት ለማስረዳት በየመንገዱ በጫት የናወዘውን ወጣት ይጠቅሳሉ፡፡

ይህም እጅግ አሳሳቢው ችግር መሆኑን መካድ አይቻልም፡፡ ጉዳዩ የሞራልና የግብረገብ እሴቶቻችን መሸርሸር አብነት እንደመሆኑ መነሳቱ አስፈላጊ ቢሆንም ኋላ ላይ ይህቺን ሀገር እንዲታደግ የሚጠይቁትም ለዚሁ ከሽፏል ለሚሉት ትውልድ ነው፡፡ ይህ አጠቃላይ የሀገሪቷ ክሽፈት ይዞ የተነሳ መፅሐፍ በመሆኑ፣ ለሌሎች ነጠላ ጉዳዮች ጭምር የመክሸፉ ትርክት ሰለባ ሲሆኑ ይታያሉ፡፡ ለዚህም ዋነኛው ምክንያት ከከሸፈች ሀገር የሚገኝ አንድም ጥሩ ነገር የለም የሚል ቃና ጎልቶ በመስተጋባቱ ነው፡፡ በተለይ ይህን ትውልድ የከሸፈ ነው የሚሉበት አንድም ማስረጃ ሳይጠቅሱ ከክሽፈቱ ጎራ መደባለቃቸው “ያለፈው ትውልድ ናፍቋቸው ይሆን?” ያስብላል፡፡ ይህ ትውልድ የእራሱ የሆኑ ቅርሶችና ማንነቶች ያሉት መሆኑ ከግንዛቤ ውስጥ የገባ አይመስልም፡፡ ትውልዱም የጠቅላላው የሀገሪቷ ክሽፈት ትርክት/ቴሲስ/ ሰለባ እንደሆነ አድርገው በአፅንኦት ገልፀዋል፡፡

በእርግጥ አፍን ሞልቶ ፕሮፌሰሩ እውነት የላቸውም ለማለት አይቻልም፡፡ ሆኖም የእሳቸውም ድምዳሜ ገና ያልታየን ትውልድ ከሸፈ ለማለት የፈጠነ ይመስላል፡፡ ይህን ለታሪክ መተው ነው የሚሻለው፡፡ ፕሮፌሰሩ እንደሚሉት፤ “ከአድዋ እስከ ማጨው ቁልቁለት ነው፤ እንዲሁም ከማይጨው እስከ ጂጂጋ የባሰ ቁልቁለት ነው፤ ውርደት ነው፤ ይህንን የቁልቁለት ጉዞ ለውጦ አቀበቱን መንገድ መቀየሱ የዛሬው ትውልድ ኃላፊነት ነው፡፡” የዚህ ትውልድ ክሽፈትም የሚመዘነው በዚሁ እርሳቸው በሰጡት የቤት ሥራ መሆን ይገባዋል፡፡

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታቸሁሳ!

ስሙኝማ…እኔ የምለው…የሸሻችሁት ነገር በየቦታው ሲመጣባችሁ አያናድዳችሁም! በተለይ የህዝብ ትራንስፖርት መኪናዎች ውስጥ… አለ አይደል… ሰላም የማይሰጣችሁን ነገር ስትሰሙ… “የት ብሄድ ነው ሰላሜ የማይረበሽብኝ!” አያሰኛችሁም? የምር…ለምሳሌ መስማት የማትፈልጉት የሬድዮ ፕሮግራም አለ እንበል፡፡ ቤት ውስጥ እሱን ፕሮግራም የከፈተ የቤተሰበ አባል እንደ ‘ፐብሊክ ኤነሚ ነምበር ዋን’ ይቆጠራል፡፡ ታዲያላችሁ…የሆነ ሚኒባስ ታክሲ ውስጥ ገብታችሁ ቁጭ እንዳላችሁ ያ ፕሮግራም በሰፊው ይለቀቅላችኋል፡፡ “እሱን ፕሮግራም ለውጥ” አትሉት ነገር የሚወዱት ሰዎች እዛው ታክሲ ውስጥ ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ እናላችሁ በሦስት ብር ከሰባ መንገድ የሠላሳ ሰባት ብር ‘አንታይ አሲድ’ ገዝታችሁ ትገባላችሁ፡፡ ወይ ደግሞ የሆነ የሙዚቃ ካሴት ተከፍቷል፡፡

ታዲያ ካሴቱ ላይ ያሉት ዘፈኖች በሙሉ የሾፌሩ የ‘አገሩ ዘፈኖች’ ይሆናሉ፡፡ እና ሾፌሩ “የአገሬ ለምለም መስክ ታወሰኝ…” ምናምን ታወሰኝ ከሚለው ዘፈን ጋር አብሮ ይዘፍናል፡፡ (ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ያው ሁላችን የትውልድ አካባቢያችንን “ለምለሟ…” “አረንጓዴዋ…” “የምድር ገነት…” ምናምን ማለት እንወዳለን፡፡ ቅልጥ ያለ ‘ሚስኢንፎርሜሽን’ ይላችኋል ይሄ ነው፡፡ አሀ ልክ ነዋ…የአንዳንዶቻችን የትውልድ መንደር ደረቅና አቧራ ከመሆኑ የተነሳ እኮ ዘመዶቻችን አረንጓዴ ቀለምን የሚያወቁት በኢትዮዽያ ባንዲራ ላይ ብቻ ነዋ! ቂ…ቂ…ቂ…) ገንዘባችሁን ከፍላችሁ በምትንቀሳቀሱበት ታክሲ የማትፈልጓቸውን ነገሮች እያቃራችሁም ለመዋጥ ትገደዳላችሁ፡፡ እናማ… አስቸጋሪ ነው፡፡

እናማ በየቦታው ስትሄዱ የሸሻችሁትን ነገር እንድታዩ ወይም እንድትሰሙ ትገደዳላችሁ፡፡ ኮሚኩ ነገር እነኛ ነገሮች ከስፍራው ጋር ምንም ግንኙነት የላቸውም፡፡ አንዳንድ ቦታማ ከሌኒን ቤተመንግሥት በስጦታ መጥተው የተረሱ የሚመስሉ መፈክሮች ግድግዳ ሞልተው ያፈጡባችኋል፡፡ የምር ግራ የሚገባኝ ነገር…ዓለም የወዝ አደሮች መሆኗ ሲቀር (እንክት አድርጐ ነዋ!) የመፈክር ለውጥ አይደረግም እንዴ! (በወዲያኛው ዘመን…“ተፈጥሮን በቁጥጥራችን ስር እናውላለን” የሚለውን መፈክር አራት ኪሎ ተሰቅሎ ሲያዩ “ድንቄም!” ያሉት ሰውዬ ሸቤ ገብተው ነበር ይባላል፡፡ ዘንድሮ “ድንቄም!” የሚያስብሉ መአት መፈክሮች አሉ፡፡ “ድንቄም!” ማለቱ…አለ አይደል…“ደግሞ ከእነማን ጋር ያስፈርጀን ይሆን!” እየተባለ ሁሉም ነገር ‘ሆድ ውስጥ’ ተከርችሞበት ቀረ እንጂ! እናላችሁ…ገንዘባችሁን ከፍላችሁ አገልግሎት የምትፈልጉበት ቦታ ሁሉ የሸሻችሁት ነገር አለቦታው መጥቶ ይደነቀርባችኋል፡፡

ቀሺሙ ምግብ ሁሉ የሙሉ ልብስ ዋጋ በሚያወጣበት በዚህ ዘመን ለመመገብ አንዱ ሬስቱራንት ትገባላችሁ፡፡ የቤቱ ባለቤቶች የፈለጉትን ሙዚቃ እስከጥግ ለቀውታል፡፡ እናንተ ምግባችሁን በሰላም፣ ጭቅጭቅ ምናምን በሌለበት ሁኔታ ነው መብላት የምትፈልጉት፡፡ እናላችሁ… የሆነ “ጉድ ስላደረግሽኝ የእጅሽን አትጪ…” ምናምን የሚል ‘ደምፕ’ ያደረገቻችሁን እንትናዬን (ነው የሚባለው… አይደል!) የሚያስታውስ ዘፈን እያምባረቀ ምግቡ እንዴት ብሎ ከጉሮሮ ይወርዳል! አይደለም አጥንቱ ሊጋጥ፣ አጥሚቱም አይወርድ! ቂ…ቂ…ቂ… ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል፣ ‘ደምፕ’ የመደራረግን ነገር ካነሳን አይቀር…ይቺን ስሙኝማ፡፡ ዘንድሮ ሙሉ ለሙሉ ‘ደምፕ’ መደረግ ቀርቷል አሉ፡፡ እናላችሁ…ነገርዬው እንደ አውሮፓ አሰልጣኞች ነገር ሆኗል አሉ፡፡

አለ አይደል…ማንቺኒ ዘንድሮ ማን ሲቲ፣ ለከርሞ ሞናኮ ደግሞ በሌላኛው እንደገና ማን ሲቲ ሊመጡ ይችላሉ፡ እና በዘንድሮ ግንኙነት “የአገሬ ወፍ ጠራችኝ…” ብላ በዛው ሄዳ የምትቀር እንትናዬ የለችም ይላሉ፡፡ ጨዋታው “የወሰደ መንገድ ያመጣል መልሶ…” አይነት ሆኗል፡፡ የእነ እንትናን ኪስ ይጭነቀው እንጂ ምን ችግር አለ! እናላችሁ…ይሄ የሚኒባሶች ነገር…አርጀት ያሉ ሚኒባሶች ወላ ሬዲዮ፣ ወላ ካሴት ማጫወቻ ስለሌላቸው ይመቹኛል፡፡ ሌሎች የሚታዩ ነገሮች ቢኖሩ የማርሹ እጀታ ተነቅሎ እንዳይወድቅ ጠፍንጎ ያሰረው ፕላስቲክ ገመድ፣ ዳሽ ቦርዱን “ወይ ንቅንቅ!” ብሎ አጣብቆ የያዘው ፕላስተር…የተሰነጠቀው የጎን መስታወት “መለያየትማ የለም!” በሚል መሀል ለመሀል ያያዛቸው የሚያብለጨልጨው አሚር ማጣበቂያ፣ የኋላ ማሳያ መስታወቷን ‘በስቅላት እንደተቀጣች’ አይነት አንጠልጥሎ የያዛት ሲባጎ…ምናምን ናቸው፡፡ የማትፈልጉት “አፈር የፈጨሁብሽ፣ እትብቴ የተቀበረብሽ መንደሬ…ናፍቆትሽ አላስቆም አላስቀምጥ አለኝ…“ምናምን አይነት ‘ሲንቴቲክ’ ዘፈን የለ…(ይሄን የሚዘፍነው ሰው የቅርብ ሞዴሏን ሌከሰስ የሚያሽከረክር እንደሆነ ግንዛቤ ይግባልንማ!) “ሳይከፍል የሚወርድ ባለጌ ነው፣” አይነት ነገር የለ…በቃ ሰላም፡፡ እናላችሁ…በየሄዳችሁበት አካባቢ ሌላ ቦታ የሸሻችሁት ነገር ይገጥማችኋል፡፡

ሠራተኞቹ ከንጉሥነት አልፈው እንደ ንጉሠ ነገሥትነት በሚቃጣቸው መሥሪያ ቤት “ደንበኛ ንጉሥ ነው” የሚል መፈክር ግድግዳ ላይ ተለጥፎ ስታዩ የፈረንሣይ አብዮት አጀማመር ምክንያትን ለማወቅ ላይብረሪ መሄድ ነው የሚያምራችሁ፡፡ ልክ ነዋ…ምናልባትም ያንን አብዮት ያስነሳው ሰው “ደንበኛ ንጉሥ ነው” ተብሎ ግድግዳ ላይ በተሰቀለ መፈክር ስለተሾፈበት የተናደደ ሊሆን ይችላላ! እናላችሁ…በሚኒባስ ታክሲዎች መሄድ የመንገድ ጉዳይ ብቻ መሆኑ ቀርቷል፡፡ እናማ… የተለያዩ እምነቶችን ‘መልእክቶችን’ በተለያዩ አቀራረቦች ወደ እናንተ ይለቀቁላችኋል፡፡ እናማ… እንደ ሹፌሩ እምነት የሚተላልፋላችሁ ‘መልእክት’ ያንኑ አይነት ይሆናል፡፡ የምር ግን አስቸጋሪ ነገር ነው፡፡ ሁሉ ሰው የየራሱ እምነት አለው…መስማት የማይፈልገውን ሊሰማ መገደድ የለበትም፡፡ የምር ግን…ሚኒባስ ታክሲዎችም ሆኑ ሌሎች የህዝብ መጓጓዣዎች የቤተ እምነቶችን ሚና ሲይዙ አሪፍ አይደለም፡፡

(በተደጋጋሚ “እሱን ነገር ዝጋው…” ምናምን በሚባል አተካሮ ችግሮች ሲከሰቱ ተመልክተናል፡፡) እናላችሁ…አንዳንዶቹ በተለያዩ መልኮች የሚቀርቡት መልእክቶች “ወዮልህ! ቀኑ ደርሶልሀል፣ እኛ ዘንድ ካልተጠጋህ…” የሚሉ አይነት ‘ማስፈራሪያዎች’ ናቸው፡፡ የመሥሪያ ቤት የአለቃ “ወዮልህ!…” የቤት ውስጥ የትዳር አጋር “ወዮልህ/ወዮልሽ…” አምልጣችሁ የለየለት “ወዮልህ!... ሚኒባስ ውስጥ ሲገጥማቸሁ አስቸጋሪ ነው፡፡ እናላችሁ…አገልግሎት ፍለጋ በምትሄዱባቸው ቦታዎች የማይመቿችሁን ነገሮች ስታዩ…አለ አይደል…አስቸጋሪ ነው፡፡ ስሙኝማ…ኮንዶሚኒየም የቤት ችግር ለማቃለል አሪፍ ነው፡፡ በርካታ ‘ብሎኮች’ ያሉባቸውን የኮንዶሚኒየም መንደሮች ስታዩ… አለ አይደል… “እነኚህ ባይሠሩ ኖሮ ይሄን ሁሉ ህዝብ ምን ይውጠው ነበር!” የሚያሰኝ ነው፡፡ ግን የኮንዶሚኒየም ኑሮን አስቸጋሪ የሚያደርጉ የእኛ ባህርያት አሉ፡፡ አቅራቢያችሁ ካለው መኖሪያ ወይ የሀይማኖት መዝሙርና ሰበካ፣ ወይ ቅልጥ ያለ የ‘ፖርኖ’ ራፕ ሙዚቃ፣ ወይ በርጫ አፎቻቸውን ‘ወደ አንድ ያዋሃደላቸው’ አሥር ሰዎች በአንድ ጊዜ ሲያወሩ…ብቻ ምን አለፋችሁ የማይሰማ ነገር የለም፡፡

በየኮንዶሚኒየሙ የሚኖሩ ወዳጆቻችን የሚያወሩን ወሬዎች አንዳንዴ የሆነ ተከታታይ የቤተሰብ ‘ሶፕ ኦፔራ’ ታሪክ ይመስላሉ፡፡ እናላችሁ… በየቦታው ውጥረቱ ሲበዛባችሁ…የሸሻችሁት ነገር መገኘት በማይገባው ቦታ ሲገጥማችሁ… አለ አይደል… ጎመን ቀቅል አሉኝ ምን ጊዜ ሊበስል ይኽንን ቀንጥሼ እዘልቀው ይመስል፣ ማለት ይመጣል፡፡ የምር እኮ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…አይደለም እኛ ግለሰቦቹ አገር ራሷ እንኳን ይህንን ‘ቀን ጥሳ ታልፍ እንደሁ’ ግራ እየገባን ያለ ጊዜ ላይ እየደረስን ነው፡፡ እግዚአብሔር ጠፍቶብኝ ብፈልግ አጣሁት ንገሩልኝ ሰዎች ቀን ያገኛችሁት ይሉ ነበር አባቶቻችን ሲቀኙ፡፡ ያን ያገኛችሁ ሰዎች ለእግዚአብሔር ብዙ አቤቱታ አላቸው ብላችሁ ንገሩልንማ! ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…የዚች አገር፣ ቀን የወጣልን፣ ቀን ያልወጣልን፣ ቀን የሚወጣልን፣ ‘ዕድላችን’ ሆኖ ቀን የማይወጣልን፣ ቀን እንዳይወጣልን የዓይናችን ቀለም መሰናክል የሆነብን ሰዎች ተብለን ምደባ ሊወጣልን የሚችል ይመስለኛል፡፡ እናማ አገልግሎት እናገኛለን ብለን በምንሄድባቸው ቦታዎች፣ በምንሳፈራቸው የህዝብ ትራንስፖርት መኪናዎች ለተጨማሪ የ‘አንታይ አሲድ’ ወጪ ማውጣት የለብንም! ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

ዕውቁ የስነልሳን ተመራማሪ ፕሮፌሰር ባየ ይማም “ቋንቋ መግባቢያ ብቻ ሳይሆን የማንነት መግለጫም ነው” ይላሉ፡፡ ይህን ፍሬ ሃሳብ የሚሽር ሌላ ማስረጃ እስካልቀረበ ድረስ የፕሮፌሰሩ አባባል ፍጹም እውነት ነው፡፡ ያለፉት የኢትዮጵያ መንግስታት ሲወቀሱበት የኖሩትና ከሚወቀሱባቸው የ “ተጨቁነናል” ቅሬታዎች አንዱም ይኸው የቋንቋ ጉዳይ ነው፡፡ እርግጥ ነው በቋንቋ እንዳይጠቀሙ ቀጥተኛ ተጽእኖ ማድረግና በሌላ አሸማቃቂ ዘዴዎች ጫና ማድረግ በማንነት ላይ የሚደረግ አደገኛ ዘመቻ ነው፡፡ በዚህ ረገድ ባለፉት መንግስታት ላይ የሚቀርቡ ቅሬታዎች ተገቢ ናቸው ብዬ አምናለሁ፡፡ (የደርግ መንግሥት በ15 የብሔረሰብ ቋንቋዎች የመሠረተ ትምህርት ዘመቻ በማካሄድ ከሌሎች ቀዳምያን መንግሥታት ልዩ መሆኑን ሳንዘነጋ)፡፡ የተባበሩት መንግስታት አካል የሆነው ዩኔስኮም ሆነ ሌሎች ዓለምአቀፍ ተቋማት በራስ ቋንቋ የመናገር መብት የሰብአዊ መብት አንዱ አካል አድርገው ይወስዱታል፡፡

ለተግባራዊነቱም ተገቢው ህጋዊ ጥበቃ መደረግ አለበት ብለው ይከራከራሉ፡፡ በ1987 ዓ.ም የፀደቀው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገመንግሥት አንቀጽ አምስትና ሰላሳ ዘጠኝም ይህንን እውነት እንዲያረጋግጡ ሆነው ተቀርፀዋል፤ ምንም እንኳ እያንዳንዱ ክልል በመረጠው ኢትዮጵያዊ ቋንቋ የመጠቀም መብት ቢኖረውም የፌዴራሉ መንግሥት የስራ ቋንቋ አማርኛ መሆኑን በግልጽ ይደነግጋል - ይኸው ህገመንግስት፡፡ አማርኛ ዛሬ የፌዴራሉ መንግሥት የሥራ ቋንቋ ከመሆን አልፎ ብዙዎች በሚሰግዱላትና በሚያመልኳት አሜሪካ ዋና ከተማ (ዋሽንግተን ዲሲም) ህጋዊ የሥራ ቋንቋ መሆን ችሏል። ከአፄ ዮሐንስ ውድቀት በኋላ ከአማራ የወጡ ግለሰቦች የፖለቲካ ስልጣን ይዘው በመቆየታቸው አማራ የሆነውን ሁሉ እንደጨቋኝ የማየት አባዜ በተለይ በየዋኃን ፖለቲከኞች ዘንድ ሲስተዋል የቆየ እውነት ነው፡፡ አሁንም የኢትዮጵያውያን አንድነት በማይዋጥላቸው በአንዳንድ ግለሰቦች ዘንድ ይኸው የቸከ ዘፈን መደመጡ ቀርቷል ማለት አይቻልም፡፡ ግን መስተዋል ያለበት ዐቢይ ቁም ነገር ያለ ይመስለኛል፡፡

በመሰሪነታቸውና ህዝብን ከህዝብ፣ ሃይማኖትን ከሃይማኖት በመነጣጠል ሴራ የሚታወቁት እንግሊዛውያን፣ ቋንቋቸው የከፋፋዮች ሃብት ስለሆነ ተብሎ ወደ ቆሻሻ ማጠራቀሚያ አልተጣለም፡፡ እንግሊዞችን አምርረው የሚጠሉት ቻይናውያንና አረቦች ሳይቀሩ እንግሊዝኛ ቋንቋን ትኩረት ሰጥተው ይማራሉ፡፡ ቻይናውያን ለምን እንግሊዝኛን መማር እንደሚፈልጉ ሲጠየቁ የሚሰጡት መልስ “የጠላታችንን ምስጢር ለማወቅ እንዲረዳን ነው” የሚል ነው፡፡ እርግጥ ነው ህዝብ የህዝብ ጠላት ሆኖ አያውቅም፡፡ እንደ ሂትለር ያሉ ልበ ድፍን መሪዎች ግን አንዱን ህዝብ በሌላው ላይ በማዝመት እንደ ቅንስናሽ ሂሳብ (ፍራክሽን) እርስበርሱ ሊያጣፉት ይችላሉ፡፡ ሆኖም እንዲህ ያለውን ጅምላ መንጋነት በመቃወም ማንኛውም ህዝብ የማንኛውም ህዝብ ጠላት አለመሆኑን በተግባር ማሳየት ይገባል፡፡ ለዚህ ደግሞ በቂ እውቀትና ልበ ሰፊነት ያስፈልጋል፡፡ በቂ ዕውቀትና ልበሰፊነት ካለ የህዝብን ወይም የገዥ መደብንና የቋንቋን መሠረታዊ ልዩነት ማወቅ አያስቸግርም፡፡ በየትኛውም ዘመንና በየትኛውም አገር ቢሆን ሰውን ሰው እንጂ ቋንቋ ጨቁኖት አያውቅም፡፡

ይልቁንም የሰብአዊ መብት ተቀናቃኞች ሰፊው ህዝብ ረግጠው መግዛት ሲጀምሩ የህዝብን ቋንቋም አብረው ይደፈጥጣሉ፡፡ ቋንቋ ብዙ ጊዜ እንደተባለውና እንደሚባለው የመግባቢያ መሳሪያ ነው፡፡ መሳሪያ በመሆኑም በአግባቡ ከተገለገሉበት ያግባባል፡፡ ያለወግ ከተጠቀሙበት ግን በግለሰቦችም ሆነ በህዝቦች መካከል ሊኖር የሚችለውን ግንኙነት ያበላሻል፤ ቋንቋን የጦር መሳሪያ ነው ብለን እንውሰደው፤ የጦር መሳሪያ በአግባቡ ከተጠቀሙበት አገርን ከወራሪ ሃይል መከላከል ያስችላል፡፡ ለዚህ ደግሞ ሰው ያስፈልጋል፡፡ ዝም ብለን ብናስቀምጠውም ዕቃ ነውና ሊበላሽ ይችላል እንጂ በራሱ ጊዜ አገርን ከጥቃት ሊከላከልልን አይችልም፡፡ ቋንቋም እንደዚሁ ነው። በአግባቡ ካልተጠበቀና ካልተገለገሉበት ይጠፋል፣ ማንነትንም ሊያጠፋ ይችላል፡፡ ኢትዮጵያ በህገመንግስቷ እንዳረጋገጠችው፤ ፌዴራላዊ መንግስቱ የዕለት ከዕለት ሥራውን የሚያከናውነው በአማርኛ ቋንቋ ነው፡፡

ህገ መንግስቱ “ተረቅቆ ፀደቀ” የሚባለው ከህዝብ በተውጣጡ ህጋዊ ወኪሎች አማካይነት ነው። ለዚህም ይመስለኛል መግቢያው ላይ “እኛ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ወደንና ፈቅደን ይህን ህገመንግሥት አጽድቀናል” ብሎ የሚጀምረው፡፡ ይህን ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ወደውና ፈቅደው ያረቀቁትንና ያፀደቁትን ህገመንግስት አክብሮ የማስከበር ኃላፊነት የእያንዳንዱ ዜጋ ቢሆንም በተለይ የፌዴራል መንግሥት ባለሥልጣናት ድርብ ኃላፊነት አለባቸው ባይ ነኝ። አንደኛ ወክለውት የመጡት ብሔር ወይም ብሔረሰብ፣ ወይም ህዝብ ስላለ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የፌዴራል መንግሥት ወኪሎች ስለሆኑ ነው። ለነገሩ ህገመንግስቱን የማክበር የዜግነት ግዴታም አለባቸው፡፡ ግን በተለይ ቋንቋን በተመለከተ ህገመንግስቱን እያከበሩት ሳይሆን በተለያየ መንገድ (የፖለቲከኞችን አባባል ልጠቀምና) እየሸራረፉት ነው - አስረጂዎቼን ላቅርብ፡፡ የሕግ አውጭው ህገወጥ ድርጊት ህግ አውጭው አካል የተዋቀረው ከዚያው ከፈረደበት “ብሔር፣ ብሔረሰብና ህዝብ” እየተባለ ከሚጠራው ነው፡፡ ያ ብሔር፣ ብሔረሰብና ህዝብ ወክሎ ሲልክ “ህገመንግሥቱን አክብሮ መብትና ጥቅሜን ያስከብርልኛል” ብሎ እንጂ ወር ሙሉ ቁጭ ብሎ የመንግስት ደሞዝ እንዲበላ ወይም ስብሰባ ባለ ጊዜ ብቻ በአጀንዳው ላይ አመነበትም አላመነበትም እጅ አውጥቶ የጐደለ ድምጽ መሙያ እንዲሆን አይደለም፡፡

በረቂቅ አዋጅነት የሚቀርብለትን ጉዳይ ጠንቅቆ ማወቅ፣ አውቆም ተገቢው ህጋዊ ተግባር እየተከናወነ መሆኑን ማረጋገጥ አለበት፡፡ የፓርቲ ዲሲፕሊን ስላለ ብቻ እሷኑ በመፍራት “ሃሳቡን የምትደግፉ” ሲባል ከእንቅልፉ ነቅቶም ቢሆን እጁን መምዘዝ ህገወጥነት ነው፡፡ በንቃት ባለመሳተፉ የተጣለበትን ህዝባዊ ውክልና አልተወጣማ! ለምሳሌ ይኸው ህግ አውጭ ያፀደቃቸውን ህገወጥ ስሞች ልጥቀስ “የኪራይ ቤቶች አስተዳደር ድርጅት” ይባል የነበረውን ተቋም “የቤቶች ኤጀንሲ”፣ “የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ባለስልጣን” ይባል የነበረውን “ፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ” ብሔራዊ ቤተመጻሕፍት ወመዘክርን “ብሔራዊ ቤተመጻሕፍትና ቤተመዛግብት ኤጀንሲ” ተብሎ ከሚኒስትሮች ም/ቤት ወይም ከአንድ ሚኒስቴር ጉራማይሌ ስም ሲቀርብለት ያለምንም ማቅማማት ተቀብሎ ያፀድቃል፡፡ ይህን ሲያደርግ ሳይ ነው ህግ ለማውጣት ህግ መጣስ የለበትም የምለው፡፡ ህግ አውጭው የፌዴራል መንግሥቱ የመጨረሻው ባለስልጣን እስከሆነ ድረስ ራሱ ያወጣቸውን የሃገሪቱን ህግና ሥርዓት በማክበር ነው ተግባሩን ማከናወን ያለበት። የፌዴራሉ መንግሥት የስራ ቋንቋ አማርኛ መሆኑን ማወቅና መቀበል፣ ተቀብሎም በስራ መተርጐም አለበት፡፡

“የምናምን ኤጀንሲ” ተብሎ ረቂቅ ሲቀርብለት “ኤጀንሲ አማርኛ ስላልሆነ ለቋንቋ ባለሙያዎች ይተላለፍና አቻ ትርጉም ይፈለግለት” ሲል አናስተውልም፡፡ ሆን ተብሎ አማርኛን ጉራይማይሌ ለማድረግ እንጂ “ኤጀንሲ” ለሚለው ቃል አቻ ትርጉም ጠፍቶለት አይደለም። በተለመደው “ድርጅት” ማለት ይቻላል፡፡ ይህ አይመጥነውም ከተባለም ከአገሪቱ ህዝብ ቋንቋዎች መፈለግና መጠቀም ተገቢም ህገመንግስታዊም ነው። ምክንያቱም ህገመንግስቱ አንቀጽ አምስት ላይ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ቋንቋዎች እኩል ህገመንግስታዊ ዕውቅና እንዳላቸው ስለሚደነግግ ነው፡፡ ለእንግሊዝኛ ቋንቋ ግን አንድም የህጋዊነት ቦታ አይሰጥም፡፡ የዛሬ አምስት ዓመት በአፍሪካ ደረጃ የተከበረውን የሁለት ሺህ ዓመት መጠናቀቅ አስመልክቶ ልዩ ልዩ ጉዳዮችን ስታዘብ ነበር፡፡ ከታላላቆቹ የመንግስት መሪዎች ጀምሮ ወደታች እስከ መጨረሻው እርከን ያሉ ንዑሳን ባለስልጣናት ድረስ ሁለት ሺህን የሚጠሩት “ሚሊኒየም” እያሉ ነበር፡፡ እንዲያውም ፕሬዚዳንት ግርማ “ሚላኒየም” የሚል ስም አውጥተውለት ነበር፡፡

ልክ ኤች አይ ቪ ኤድስን “ኤች ቪ አይ” ብለው እንደሚጠሩት ማለት ነው፡፡ በወቅቱ ከተገረምሁባቸው የመንግስት ተቋማት አንዱ የሰባ ሁለት ዓመቱ (ያኔ ስልሳ ሰባት ዓመቱ ነበር) አዲስ ዘመን ጋዜጣ “የሚሊኒየም ገጽ” ብሎ ቋሚ አምድ ሲከፍት በኦሮሚፋ የሚታተመው በሪሳ ጋዜጣ ግን “በርኩሜ” የሚል ቆንጆ ቃል ተጠቅሞ ማየቴ ነው፡፡ በርኩሜን “ቆንጆ ቃል” ያልሁት ትርጉሙ ሺህ ዓመት ማለት ሲሆን ኢትዮጵያዊም ህገመንግስታዊም ቃል ስለሆነ ነው፡፡ የበዓሉን ዓላማም በአግባቡ ገልጿል፡፡ ከዚህ በላይ አፍሪካውያን “የራሳችን በዓል ነው” ብለው የወሰኑትን ጉዳይ ኢትዮጵያዊ ቃል ቢጠፋ እንኳ (አልጠፋም እንጂ) ከሌላ አፍሪካዊ ቋንቋ መጠቀም ይቻል ነበር፡፡ ለምሳሌ በርኩሜ በጣም ገላጭና አጭር ቃል ሲሆን ሺህ ዓመት፣ ዓምኣት፣ ወዘተ ማለት ይቻል ነበር፡፡ ነገሩ “ሳይቸግር ጤፍ ብድር” መሆኑ ነው። ወይም እኒያኑ “የምናመልካቸውን” ፈረንጆች ለማስደሰት ሊሆን ይችላል፡፡ እናም ህዝብን ወክሎ የተቀመጠው ህግ አውጭ የሚያወጣቸው ህጐች በይዘት ብቻ ሳይሆን በቋንቋም ህገመንግስቱ የሚደነግገውን ስርዓት ጠብቀው መውጣታቸውን የመቆጣጠር ህጋዊ ኃላፊነት አለበትና ተግባራዊ ሊያደርገው ይገባል ባይ ነኝ፡፡

የጠቅላይ ሚኒስትሩ ህገወጥ መግለጫ ነፍሳቸውን ይማርና ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ኢትዮጵያን ወክለው ሲናገሩ የፈረንጅ አፍ ይቀናቸው ነበር፡፡ አንዳንድ ሰዎችም እንግሊዝኛቸውን ሲያደንቁላቸው ሰምቻለሁ፡፡ ግን እንግሊዝኛ መናገርኮ የአዋቂነት መለኪያ ሊሆን አይችልም፡፡ በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ስር የነበሩ የኬንያ፣ የደቡብ ሱዳንና በአገራችንም የጋምቤላ ገበሬዎች ከቋንቋ ምሁራን የተሻለ እንግሊዝኛ ይናገራሉ፡፡ ግን ያው እንደ አማርኛ ተናጋሪው፣ እንደ ኦሮምኛ ተናጋሪው ወይም እንደ ሱማሊኛ፣ አፋርኛ፣ወይም ስልጢኛ ተናጋሪው ገበሬዎች እንጂ የሊቃውንት ቁንጮዎች አይደሉም፡፡ በኮሙኒዝም ወቅት በአውሮፓ የኬጂቢ ከፍተኛ ወኪል የነበሩት የዛሬዋ ሩሲያ ፕሬዚዳንት ፑቲን እንግሊዝኛ አቀላጥፈው ይናገሩ ነበር፤ አሁንም ችሎታው አላቸው፡፡ በእንግሊዝኛ ችሎታቸውም ነው የሃያሉ የስለላ ተቋም ከፍተኛ ባለሙያ ሆነው የተመደቡት፡፡ ግን የሩሲያ ፕሬዚዳንት ሆነው ከተሰየሙ በኋላ በሩስኪ ቋንቋ ውስጥ ቢሞቱ እንኳ አንዲት የእንግሊዝኛ ቃል አይጨምሩም፡፡ ምክንያቱም የሩሲያ የሥራ ቋንቋ ሩስኪ እንጂ እንግሊዝኛ አይደለማ! ጀርመኖች በራሳቸው ቋንቋ ካልሆነ መንገድ የጠፋበት እንግዳ ሰው ቢጠይቃቸው እንኳ በቋንቋቸው ካልሆነ አይጠቁሙም፤ ፈረንሳዮችም ለቋንቋቸው እጅግ ጠንቃቆች ናቸው፡፡

ፕሬዚዳንት መንግስቱ ኃ/ማርያምም ቢሆኑ እንግሊዝኛ ቋንቋ በደንብ መናገር እየቻሉ ከማንኛውም አገር መሪ ጋር ሲነጋገሩ በብሔራዊ ቋንቋቸው እንደነበር የረጅም ጊዜ አስተርጓሚያቸው አቶ ግርማ በሻህ ለግል መገናኛ ብዙኃን መግለጻቸውን አስታውሳለሁ፡፡ እንዲያውም “አንድ ጊዜ ፕሬዚዳንቱ ከሆነ አገር መሪ ጋር ሲወያዩ የተሳሳተ ትርጉም በመስጠቴ ግርማ! እንደዚያ አይደለም ያልሁት፡፡ አሁንም እንዲህ ብለህ አስተካክለህ ንገረው ብለው አርመውኛል” ብለዋል፤ የብዙ ቋንቋዎች ተናጋሪ የሆኑት አቶ ግርማ በሻህ፡፡ እዚህ ላይ ልብ ማለት የሚያሻው ነገር ፕሬዚዳንት መንግስቱ በአማርኛ የሚናገሩት እንግሊዝኛ አልችል ብለው ሳይሆን ለሀገራቸውና ለራሳቸው ክብር በመስጠታቸው መሆኑን ነው። “ራሱን ያቀለለ አሞሌ ባለ ዕዳ አያከብረውም” የሚባለው የዚህ ዓይነቱ የማንነት ጉዳይ ሲያጋጥም ይመስለኛል፡፡ በደርግ ዘመንማ እንዲያውም የከፍተኛ ትምህርት ሁሉ በብሔራዊ ቋንቋ እንዲሰጥ ዝግጅቱ ጦፎ እንደነበር በቂ ማስረጃዎች አሉ፡፡

የቀድሞው ንጉሥ ኃ/ሥላሴም ቢሆኑ እንግሊዝኛ አጥርተው ይናገሩ እንደነበር “አዶልፍ ፓርለስክ” የተባለ ቸኮዝሎባኪያዊ “የሐበሻ ጀብዱ” በተባለው መጽሐፉ ላይ ገልጿል፡፡ ግን ንጉሡ የትም ቦታ ይናገሩ የነበረው በብሔራዊ ቋንቋቸው አማርኛ ነበር፡፡ አማርኛ ግራ ይገባው የጀመረው በዘመነ ኢህአዴግ ይመስለኛል፡፡ አንድ ወቅት አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ባዘጋጀው ረቂቅ መሪ ዕቅድ ላይ ውይይት አካሂዶ ነበር፡፡ በውይይቱ ላይ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም ተሳትፈዋል፡፡ ይሁን እንጂ ሙሉ ንግግራቸውን በእንግሊዝኛ ነበር ያደረጉት፡፡ ግን ለማን? ለምን ዓላማ? ግልጽ አይደለም፡፡ ስለ ቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር (ከቋንቋ ጋር በተያያዘ) ብዙ ማለት ይቻላል፡፡ ግን የአገራችን አባባል “ሙት ወቃሽ አታርገኝ” ይላል፡፡ እኔም ለአባባሉ ልገዛና በዚሁ ልለፋቸው፡፡ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ሥራቸውን የጀመሩት “የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር ሌጋሲ ያለምንም ማወላወል አስፈጽማለሁ” በማለት ቃል ገብተው ነው፡፡ እውነትም በደንብ ተክተዋቸዋል፡፡

ለመሆኑ “ሌጋሲ” የሚለው ቃል አቻ ትርጉም የለውም? “ውርስ፣ ፈለግ፣ ዕቅድ፣ ራዕይ፣ ውጥን” ማለት ሊሆን አይችልም ይሆን? አማርኛ ቃል ቢጠፋለትስ ወላይትኛ፣ ጌዴዎኛ፣ ሲዳምኛ ወዘተ ሊገኝለት አይቻልም? ከሁሉ የገረመኝ በስራቸው የሾሟቸው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች ማዕረግ ነው (እሳቸው በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ ነው የተሾሙት እንጂ ምክትል ጠ/ሚኒስትራችን አንድ ብቻ ናቸው ብለውናል) የዚህ ዓይነት ሹመት ህገመንግስታዊ ነው አይደለም? የሚለውን ፍሬ ነገር እናቆየውና የማዕረጋቸው ማጀቢያ ቃል በእጅጉ ያስፈራል፡፡ ምክንያቱም “የዚህ ክላስተር አስተባባሪ፣ የዚያ ክላስተር አስተባባሪ” የሚል ነው፡፡ ካልጠፋ ስም “ክላስተር”ን ምን አመጣው? ለዓመታት የኖርነው በዘግናኝ ጦርነት ውስጥ ነው፡፡ ከደርግም ሆነ ዛሬ ሁለት መንግስታት ካቋቁሙት የዚያኔዎቹ አማጽያን ይሰጥ የነበረው መግለጫ “ደርግ ወይም ሻዕቢያ ወይም ወያኔ ሰላማዊውን ህዝብ በክላስተር ቦንብ ጨፈጨፈ” የሚል ነበር፡፡ ስለሆነም ክላስተር የማህበራዊ አገልግሎት አስተባባሪነትን ሳይሆን አስፈሪነትን፣ ነፍሰ ገዳይነትን፣ ስጋትንና መከራን ነው ሊያስታውሰን የሚችለው፡፡ ለዚህ ሳይሆን ይቀራል በአንዳንድ አካባቢዎች “የአባት ክፉ የስም ድሃ ያደርጋል” የሚባለው? መሪኮ የሁሉ ነገር መሪ ነው፡፡

ለምሳሌ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ በርኩሜን ወይም ሺህ ዓመታችንን ስናከብር ከባለቤታቸው ክብርት ወይዘሮ አዜብ ጋር በባህላዊና ብሔራዊ ልብሳቸው ተንቆጥቁጠው ነበር ያከበሩት፡፡ ከማግስቱ ጀምሮ የፌዴራልና የክልል ባለስልጣናት እንዲሁም የወረዳና የቀበሌ ሹማምንት ሳይቀሩ በዚሁ ባህላዊ ልብስ መዋብ ጀመሩ፡፡ ለማንነታቸው ትኩረት በመስጠታቸውም ሊወደሱ እንጂ ሊወቀሱ አይገባም፡፡ እንደዚህ ሁሉ ለቋንቋችንም መሪዎች ሲጠነቀቁ ቢታዩ፣ ሌላው ባለስልጣንና ድምሩ ህዝብ ለራሱ ሃብት ትኩረት ሊሰጥና በማንነቱ ሊኮራ ይችላል፡፡ ጉራማይሌ ቋንቋ ያመጣው ጣጣ ብዙ ነው። የልጆች፣ የንግድ ተቋማት፣ የግል ት/ቤቶችና አንዳንድ አደባባዮች ሳይቀሩ “በኢትዮጵያዊ ስም ብትጠሯቸው ትከስራላችሁ” የተባሉ ይመስል ከተማችንን አስጠሊታ አድርገዋታል፡፡

ጀግኖች ወላጆቻችን አጥንታቸውን ማገርና ግድግዳ አድርገው ሃገራችንን በባዕዳን ባያስወርሯትም፣ እኛ ግን ወደንና ፈቅደን ለባዕዳን መጤ ባህልና አስተሳሰብ ህሊናችንን ለጭዳነት አቅርበናል፡፡ “ዲያስፖራ አደባባይ፣ ቦብማርሌይ አደባባይ፣ ካርል ሃይንዝ አደባባይ፣ ቸርችል ጐዳና፣ ካኒንግሃም መንገድ ወዘተ” በመንግሥት የተሰየሙ የባዕዳን መታሰቢያዎች ናቸው፡፡ እርግጥ ነው እነዚህ ሰዎች ለሀገሪቱ በአጠቃላይ፣ ወይም ለመሪዎች በተለይ የከፈሉት ውለታ ሊኖር ይችላል፡፡ ግን በተለያየ መንገድ ለሀገራቸው መስዋዕት የሆኑ ጀግኖቻችንን የት አገር ወስደን እንዲታወሱ እናድርግ? የኢፌዴሪ ህገመንግስት፤ የፌዴራሉ መንግሥት የሥራ ቋንቋ አማርኛ ነው ይላል፡፡ የፌዴራሉ መንግሥት መቀመጫ ደግሞ አዲስ አበባ ነው።

ታዲያ በፌዴራሉ መንግሥት ጉያ ስር የተወሸቁ አንዳንድ የግል ት/ቤቶች “አማርኛ መናገርና ድንጋይ መወርወር ክልክል ነው” እስከማለት ሲቀናጡ፣ አገሪቱ የትምህርት ሚኒስቴርና የፍትሕ ተቋማት አሏት ወይ አያሰኝም? በአፍ መፍቻ ቋንቋ መማርኮ ዓለምአቀፍ ተቀባይነት ያገኘ ሰብአዊ መብት ነው። ስለሆነም እባካችሁ መሪዎቻችን፤ ቋንቋችሁንና ቋንቋችንን አፍቅሩ! በማንነታችሁ ኩሩ! የሀገሪቱን ህግጋት አክብሩ! አለዚያ አትወክሉንማ!!

Published in ህብረተሰብ
Page 6 of 14