የዛሬ አስር ዓመት የአስራ ሰባተኛ ዓመት የልደት በአሏን ለማክበር አንድ ቀን ሲቀራት ለስራ እንደወጣች አልተመለሰችም- አሜሪካዊቷ አማንዳ ቤሪ፡፡ ደብዛዋ ከመጥፋቱ በፊት ግን እህቷ ጋ ደውላ ከምትሰራበት ቦታ ወደ ቤት የሚመልሳት መኪና እንዳገኘች ተናግራ ነበር፡፡ የ14 ዓመቷ ጂና ደግሞ የዛሬ ዘጠኝ ዓመት ትምህርትቤት እንደሄደች አልተመለሰችም፡፡ ናይት ከሁለቱ ቀደም ብላ በ2002 ዓ.ም ደብዛዋ የጠፋ የ20 አመት ወጣት ነበረች፡፡ ሶስቱ ሴቶች በተለያዩ ጊዜዎች የጠፉ ቢሆንም ተመሳሳይ ታሪክ አላቸው፡፡ ሶስቱም ፔድሮ ካስትሮ በተባለ ግለሰብ ታግተው በመኖሪያቤቱ ምድርቤት ውስጥ የተለያዩ ስቃዮችን አሳልፈዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋለው ግለሰቡ ሴቶችን በመኪና ልሸኛችሁ (ሊፍት ልስጣችሁ) እያለ ነበር ወጥመድ ውስጥ ያስገባቸው፡፡

ሶስቱ ሴቶች እንደታገቱ በተለያዩ ክፍሎች ተነጣጥለው እንዲቀመጡ ያደረገ ቢሆንም በኋላ ላይ አንድ ላይ እንዳደረጋቸው ባለታሪኮቹ ይናገራሉ፡፡ በዓመታት የእገታ ቆይታቸው ተገደው ተደፍረዋል ፤ ለሳምንታት ምግብ ተከልክለዋል፤ ድብደባ ተፈፅሞባቸዋል ፤ በሰንሰለትም ታስረዋል፡፡ በፖሊስ መረጃ መሰረት ፤ ከሴቶቹ አንዷ አምስት ጊዜ ተገዳ ተደፍራ አምስት ጊዜ የፅንስ መጨናገፍ ደርሶባታል - በተፈፀመባት ድብደባ እና የምግብ ክልከላ የተነሳ፡፡ የሴቶቹ የመሰወር ምስጢር በቅርቡ እስኪታወቅ ታዲያ የተለያዩ ግለሰቦች ተጠርጥረው ፍርድ ቤት ቀርበዋል፡፡ እንስቶቹ ሞተዋል በሚል ግምትም ፖሊስ አስከሬናቸውን ለማግኘት ያልፈነቀለው ድንጋይ አልበረም፡፡ በቅርቡ ግን ሁሉም በህይወት ተገኝተዋል፡፡

ታጋቾቹ በእነዚህ ሁሉ ዓመታት ከክፍላቸው ወጥተው ውጭውን ያዩት አንድ ጊዜ ብቻ ነው - ያውም እዚያው ቤት ግቢ ውስጥ፡፡ ሰዎች ማንነታቸውን እንዳይለዩዋቸው መነጽር፤ ኮፊያ እና ዊግ እንዲጠቀሙ ተገደው እንደነበርም አስታውሰዋል - ለፖሊስ በሰጡት ቃል፡፡ በአሜሪካን ኦሃዮ ግዛት፤ ክሌቭላንድ ውስጥ ለ10 አመት ገደማ ታግተው የቆዩት ሴቶች ባለፈው ሰኞ ነው ነፃ የወጡት- ያገታቸው ግለሰብ ከቤት ሲወጣ አማንዳ ቤሪ ባሰማቸው የድረሱልን ጥሪ፡፡ ከዚያ በፊት ግን እንዲህ ያለ ሙከራ አድርገው እንደማያውቁ አማንዳ ለፖሊስ ገልፃለች፡፡ በመጀመርያ ሙከራዋ ውጤታማ መሆናም ጀግና አሰኝቷታል፡፡ ወደ ማገቻው መኖርያ ቤት የገቡት ሶስቱ ሴቶች ብቻ ቢሆኑም ሰሞኑን ነፃ ሲወጡ ግን የውጭውን ዓለም የማታውቅ የስድስት አመት ህፃንም አብራ ነበረች፡፡ ልጅቷ የቤሪ እንደሆነች የታወቀ ሲሆን አባቷ ማን እንደሆነ ለማወቅ ግን ምርመራ ይካሄዳል ተብሏል፡፡

የቤሪን ጩኸት ሰምቶ ሴቶቹን ነፃ እንዲወጡ የረዳቸው ቻርለስ ራምሴ የተባለ የካስትሮ ጎረቤት ነው፡፡ በዚህ መልካም ሥራውም ከመላው አሜሪካ ከፍተኛ አድናቆት እየጎረፈለት መሆኑ ታውቋል፡፡ ራምሴ የሚሰራበት ሬስቶራንት የፌስቡክ ገፅ ላይ የሰፈረው ፅሁፍ እንዲህ ይላል “በባልደረባችን መልካም ተግባር እጅግ ኩራት ተሰምቶናል፡፡ እሱ የክሌቭላንድ ጀግና ነው፡፡” ራምሴ ስለሁኔታው ሲገልፅም፤ “ድምፅ ሰምቼ ከቤቴ ስወጣ አንዲት ሴት ከጎረቤት ካለው ቤት ለመውጣት ስትታገል አገኘሁ፡፡ በሩን እየደበደበች ያለማቋረጥ የምትጮኸውን ሴት ከዚህ በፊት አይቻት አላውቅም፡፡ “እኔ ታግቼ ነው፡፡ እዚህ ቤት ለአመታት ተዘግቶብኝ ኖሬያለሁ፡፡ አሁን ነፃ መውጣት እፈልጋለሁ” አለችኝ ፡፡ ለምን 911 አትደውይም ስላት መውጣት እንደምትፈልግ አጥብቃ ነገረችኝ ፡፡ እኔና ሌላ ሰው በሩን በመክፈት ተባበርናት፡፡ እናም 911 በመደወል እኔና ቤሪ ሁኔታውን አስረዳን፡፡ ፖሊስ ሲመጣ ሌሎች ሁለት ሴቶች ውስጥ እንዳሉ ገልፃ ሁሉም ነፃ ወጡ” ብሏል፡፡ ራምሴ በአጋችነት የተጠረጠረውን ጎረቤቱን እንዲህ ያለ ተግባር ይፈፅማል ብሎ አስቦ አያውቅም፡፡

“ስለጎረቤቴ ምንም የተለየ ነገር አላውቅም ነበር፡፡ ብዙ ምሽቶችን ስጋ እየጠበስንና ሳልሳ ሙዚቃ እየሰማን አሳልፈናል፡፡ ግቢው ውስጥም ሁልጊዜ ከውሾቹ ጋር ሲጫወት ነው የማየው፡፡ ዛሬ ካየሁት ውጪ የሚያስገርም ነገር ሲያደርግ አይቼ አላውቅም” በማለት መገረሙን ገልጿል፡፡ የአውቶቡስ ሾፌሩ ካስትሮ፤ የፖርቶሪኮ ተወላጅ ሲሆን የላቲን ባንድ የሙዚቃ ተጫዋች ነበር፡፡ የዛሬ ስምንት ዓመት ገደማ በአሁኑ ወቅት አብራው በማትኖር ሚስቱ የድብደባ እና የግድያ ዛቻ ክስ ቢቀርብበትም ክሱ ውድቅ ተደርጓል፡፡ የፖሊስ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በ2000 እና በ2004 ዓ.ም ፖሊስ በደረሰው ጥቆማ በካስትሮ ቤት ላይ ፍተሻ አድርጎ ነበር፡፡ ነገር ግን ምንም ፍንጭ ሳያገኝ ተመልሷል፡፡ አሁን የሶስቱ ሴቶች ህይወት ተቀይሯል፡፡ አማንዳ ቤሪ የ27 አመት ሴት እና የስድስት አመት ልጅ እናት ሆናለች፡፡ እናቷን በህይወት ለማግኘት አልታደለችም፡፡

በልጃቸው ድንገተኛ መሰወር ልባቸው ክፉኛ የተሰወረው እናቷ ከጠፋችበት እለት አንስቶ ህይወታቸው እስክታልፍ ድረስ ያለመታከት ልጃቸውን ሲያፈላልጉ ቆይተዋል ሆኖም የልጃቸውን ዓይን ሳያዩ በደረሰባቸው የጤና እክል ህይወታቸው አልፏል፡፡ ሚሸል ናይት የ30 አመት ሴት ሆናለች፡፡ እሷ ከታገተች በኋላ የተወለደች አዲስ እህት አግኝታለች፡፡ እናቷ በሰጠችው አስተያየት፤ “ልጄን በህይወት ማግኘቴ ታላቅ ስጦታ ነው፡፡ ቶሎ እንድታገግም አግዛታለሁ” ብላለች፡፡ ከትምህርት ቤት ወደቤት ለመመለስ ዘጠኝ አመታት የፈጀባት ጂና፤ ቤተሰቦቿን የተቀላቀለችው የ23 አመት ወጣት ሆና ነው፡፡ በእነዚያ ዓመታት ብዙ ስቃዮችን ብታሳልፍም ፊቷን በሹራቧ ሸፍና የአውራ ጣቷን ወደ ላይ በመቀሰር ዳግም ከቤተሰቧ ጋር መቀላቀሏ የፈጠረባትን ደስታ ገልፃለች፡፡

ሦስቱም ሴቶች ከደረሰባቸው የአካልና የሥነልቦና ጉዳት ለማገገም ሆስፒታል ገብተው የነበረ ሲሆን ሁለቱ ህክምናቸውን አጠናቀው ሲወጡ እናቷን በሞት ያጣችው ናይት ግን አሁንም እዚያው ትገኛለች፡፡ መርማሪዎች ወደ ሁለት መቶ የሚጠጉ ማስረጃዎችን ከካስትሮ ቤት ሰብስበዋል፡፡ የክሌቭላንድ ከንቲባ ፍራንክ ጃክሰን፤ ሶስቱ ሴቶች በህይወት መገኘታቸው እንዳስደሰታቸው ገልፀው ሆኖም ያልተመለሱ ብዙ ጥያቄዎች አሉ ብለዋል፡፡ ለምን ተወሰዱ? እንዴት ተወሰዱ? ይህን ያህል ጊዜስ ያሉበት እንዴት ሳይታወቅ ቀረ የሚሉና ሌሎችም፡፡ ከንቲባው እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ ምርመራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ቃል ገብተዋል፡፡ ምንም እንኳን ቤሪ እናቷን ለማየት ባትታደልም እናት ለመሆን በቅታለች፡፡ ጂና እና ናይት ደግሞ ከእናቶቻቸው ጋር ለመገናኘት ችለዋል፡፡ እናም ሦስቱ ሴቶች ከአስር ዓመት እገታ በኋላ ነፃ መውጣታቸው ነገ ለሚከበረው “የእናቶች ቀን” መልካም ስጦታ ሆኖላቸዋል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

በርካታ አረንጓዴ ዩኒፎርም የለበሱ ወጣቶች ጥቅጥቅ ባለ የባህር ዛፍ ደን ውስጥ ስንመለከት፣ ከትምህርት ቤት የፎረፉ ተማሪዎች እንጂ መኪና አጣቢዎች አልመሰሉንም፡፡ ወደ ቦታው ቀረብ ስንል ግን ተረኞቹ መኪና አጣቢዎች ደኑ ስር አረፍ ካሉት ዩኒፎርም ለባሾች ጋር ተመሳሳይ የደንብ ልብስ የለበሱ መሆናቸውን አስተዋልን፡፡ እነዚህ ወጣቶች “ይገርማል የመኪና” እጥበት አባላት ናቸው፡፡ ከስምንት ዓመት በፊት ትምህርቱን እስከ 12ኛ ክፍል ያጠናቀቀው ወጣት ስንታየሁ አየለ፤ መንገድ ላይ መኪና በማጠብ ነው ሥራ የጀመረው። ትንሽ ቆይቶም ሌላ ልጅ ተጨመረ፡፡

ነገር ግን መኪናው የታጠበበት ውሃና ዘይት አካባቢን በመበከል ችግር ፈጠረ፡፡ የአካባቢው ፖሊሶችም ስንታየሁና ጓደኞቹን ማባረርና መያዝ ሥራቸው ሆነ፡፡ ወጣቶችም እየታሠሩ መፈታት የዕለት ተዕለት ሥራቸው እስኪመስላቸው ተደጋገመ፡፡ “በወቅቱ እኛ ብር ማግኘታችንን እንጂ የመኪና እጣቢው ጉዳት እንዳለው አላሰብንም ነበር” ይላል የማኅበሩ መስራች ወጣት ስንታየሁ አየለ፡፡ በመንገድ ላይ የመኪና እጥበት የተነሳ ታስረው በከባድ ማስጠንቀቂያ ከተፈቱ በኋላ፣ ስንታየሁና ጓደኞቹ ሥራ ፈተው መቆየታቸውን አጫውቶኛል፡፡ “ምን ልሥራ እያልኩ ሳሰላስል ለመኪና እጥበቱ ለምን መፍትሔ አልፈልግም የሚል ሃሳብ በአዕምሮዬ ሽው አለ” ይላል፡፡ ይኼኔ ነው “Water recycling from Car Washing” የተሰኘ ባለ 23 ገጽ ፕሮፖዛል ጽፎ ለፌደራል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ያስገባው። ባለስልጣኑ ፕሮጀክቱን አገላብጦ ከተመለከተ በኋላ፣ ባለሙያ በመመደብ በፕሮፖዛሉ ላይ መጠነኛ ማስተካከያ ተደርጐ ወደ ሥራ እንዲገቡ አሁን የሚሠሩበትን አንድ ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ለሙከራ እንደተሰጣቸው ወጣቱ ይናገራል፡፡ በዚሁ መሠረት በ1999 ዓ.ም “ይገርማል የመኪና እጥበት አገልግሎት” ተመሠረተ፡፡

ፕሮጀክቱ ውሃን በማጣራት መላልሶ መጠቀም ሲሆን ይህ የመኪና እጥበት አገልግሎት አዲሱ ገበያን አልፎ በሱልልታ መንገድ በተለምዶ ድልበር እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ላይ ይገኛል፡፡ ወጣት ኃይለሚካኤል ላንቴ በ“ይገርማል የመኪና እጥበት አገልግሎት” ሠራተኛ ነው፡፡ ሥራውን ከጀመረ ሁለት ዓመት ሆኖታል፡፡ “ተወልጄ ያደግሁት ጅሩ የሚባል አገር ነው፡፡ ሥራ ፍለጋ አዲስ አበባ ስመጣ ሰዎች ከስንታየሁ ጋር አስተዋወቁኝ” የሚለው ኃይለሚካኤል፤ ምንም እንኳን ከዚያ በፊት መኪና አጥቦ ባያውቅም ለአንድ ሳምንት ያህል በተግባርና በቪዲዮ የተደገፈ ስልጠና ወስዶ አሁን ጐበዝ መኪና አጣቢ ለመሆን መቻሉን ይናገራል፡፡ “ስልጠናው መኪና ማጠብ ብቻ አይደለም” የሚለው ወጣቱ፤ ስለ መልካም ስነምግባር፣ ስለ ደንበኛ አያያዝና መስተንግዶ፣ በሥራ ላይ ስለመተባበርና ስለእርስ በእርስ ተግባቦት ስንታየሁ እንዳሠለጠናቸው ይናገራል፡፡ “በአሁኑ ሰዓት የምፈልገውን ካደረግሁ በኋላ የተረፈኝን ብር ስንታየሁ ባስተማረኝ መሠረት እየቆጠብኩ አራት ሺህ ብር ያህል አጠራቅሜያለሁ” ብሏል፡፡

በሁለት አባላት የተመሠረተው ማኅበር፣ በአሁኑ ወቅት 54 አባላት ያሉት ሆኗል፡፡ በየቀኑም በርካታ መኪኖች ያጥባሉ፡፡ ውሃን እያጣሩ መልሶ በመጠቀም ዘዴ መኪኖች ሲታጠቡ የሚወርደው ቅባትና ዘይት አንድ ቦታ ተንሳፎ ይቀራል፤ ጭቃው ይዘቅጣል፤ ውሃው ተመልሶ ወደማጣሪያው ይገባና ቢያንስ ለስምንት ዙር አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ወጣቶቹ መኪና የሚያጥቡበት ውሃ እጅግ ኩልል ያለና ንፁህ ሲሆን ስምንት ጊዜ መኪና ታጥቦበታል ብሎ ለማመን ያስቸግራል፡፡ የማህበሩ መስራች ወጣት ስንታየሁ እንዳጫወተን፤ ቦታውን ከአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ከወሰዱ በኋላ፣ ከአዲስ ብድርና ቁጠባ 10ሺህ ብር በመበደር የማጣሪያውን ዝርጋታ አካሄዱ፡፡ “ወደ አካባቢው የሚለቀቅ አንዳች ቆሻሻ የለም” ይላል ወጣት ስንታየሁ፡፡ ሌላው ቀርቶ ከመኪናው የሚወጣው ዘይትና ቅባት በሊትር ሦስት ብር ከሰባ አምስት ሳንቲም ይሸጣል፡፡ “እንዴት?” የሚል ጥያቄ አነሳሁ፡፡

“የጠለለውን ዘይትና ቅባት በአብዛኛው የሚገዙኝ ኮንስትራክሽን ሥራ ያላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ አልፎ አልፎ ሻወር ቤት ያላቸውም ይወስዱታል” የሚለው የፕሮጀክቱ ጠንሳሽ፤ “የኮንስትራክሽን ሠራተኞቹ ፓኔል ሲሰሩ ሲሚንቶ ልክክ አድርጐ እንዳይዝባቸው የተቃጠለውን ዘይትና ቅባት ይቀቡታል፡፡ ባለሻወር ቤቶቹ ደግሞ በዚሁ ዘይት ላይ ዲናሞ ገጥመው ውሃ ያሞቁበታል” ብሏል፡፡ በስፍራው በመኪና እጥበት ሥራ ላይ ተፍ ተፍ ሲል ቆይቶ ፋታ ሲያገኝ ያናገርኩት ወጣት ኃይሌ በየነ፤ ሥራ ከጀመረ አራት ዓመት ሆኖታል፡፡ ከመኪና እጥበት ጋር የተዋወቀው በዚሁ ስፍራ ነው፡፡ ላለፉት አራት ዓመታት መኪና ሲያጥብ ጐን ለጐን መንጃ ፈቃድ ለማውጣት ያደረገው ጥረት ተሳክቶለታል። “ስራው ደስ ይላል፣ የሠራ ሰው የሚያገኝበት ነው። እኔም ከመሰረታዊ ፍላጐቴ አልፌ መንጃ ፈቃድ አውጥቻለሁ፡፡” የሚለው ኃይሌ፤ በቀጣይ ወደ ሹፍርና ሙያ ለመግባት እቅድ አንዳለው ይናገራል፡፡ “እዚህ ከምትመለከቻቸው ውስጥ ስምንት ወጣቶች መንጃ ፈቃድ አውጥተዋል፡፡

የማታ ትምህርት የሚማሩም አሉ” ይላል ሊቀመንበሩ ስንታየሁ፡፡ የመኪና እጥበት ዓለም አቀፍ ሥራ እንደሆነ በፅኑ የሚያምነው ስንታየሁ፤ “በእኛ አገር ለመኪና እጥበትና አጣቢ የሚሰጠው ግምት ዝቅተኛ ቢሆንም እኛ ግን የሰውን አመለካከት የሚቀይር ሥራ እየሰራን ነው” ብሏል፡፡ መኪና ከሚያጥቡት ሠራተኞች ለየት ያለ የደንብ ልብስ ለብሷል፡፡ ደብተርና እስክሪብቶ ይዞ ዙሪያውን ይንጐራደዳል። ከሁኔታው መኪና አጣቢ እንዳልሆነ ብረዳም የማህበሩ ሠራተኛ መሆኑ ግን አልጠፋኝም፡፡ ተሾመ ጠርዝነህ ይባላል፡፡ እርሱም በስፍራው ለአምስት ዓመት ሰርቷል፡፡ ከመኪና አጣቢነት ተነስቶ የሠራተኞቹ ሱፐርቫይዘር ሆኗል፡፡ ከጅሩ የመጡ ጓደኞቹ ጠቁመውት መኪና እጥበቱን የተቀላቀለው ተሾመ፤ “አገሬ እያለሁ ትምህርቴን አቋርጬ ቦዘኔ ነበርኩ” ብሏል፡፡ ያቋረጠውን ትምህርት በማታ ቀጥሎ አሁን ስምንተኛ ክፍል ደርሷል፡፡ ሁሉም ተፍ ተፍ ይላል፣ ይጣደፋል፣ ግማሹ ያጥባል ግማሹ ይወለውላል፣ ግማሹ የሞተሩን ፓምፕ ይቆጣጠራል፡፡ መኪናው በሚታጠብበትና ውሃው በሚጣራበት ቦታ ዙሪያ በሚወርደው ውሃ የሚበቅል ጐመን፣ ቃሪያ፣ ድንች፣ ቆስጣና መሰል የጓሮ አትክልቶችን ተመለከትኩና ጠየቅሁት። “እነዚህ አትክልቶች ለሽያጭ የሚውሉ ሳይሆኑ ሠራተኞች አብስለው እዚሁ የሚጠቀሟቸው ናቸው” የሚለው ስንታየሁ፤ ውሃው ይሄን ያህል ጤናማ እንደሆነ አጫውቶኛል፡፡

የማኀበሩ ጸሐፊ የሆነው ወጣት ብሩክ ተስፋዬ፤ ከCPU ኮሌጅ በአካውንቲንግ ከተመረቀ በኋላ በ “ይገርማል የመኪና እጥበት” በጸሐፊነት መቀጠሩን አጫውቶኛል፡፡ “መኪና እጥበት ቤት ነው የተቀጠርኩ ስላቸው ቤተሰቦቼ ደስተኛ አልነበሩም” ያለው ብሩክ፤ መጥተው ስፍራውን ከጐበኙ በኋላ ሐሳባቸውን እንደቀየሩ አጫውቶኛል፡፡ “እዚህ ስፍራ ተቀጥሬ ደሞዝ ከመቀበል ባለፈ ከስንታየሁና ከባልደረቦቹ በርካታ ቁምነገሮችን ተምሬያለሁ” የሚለው ወጣት ብሩክ፤ ከደሞዙ ላይ በወር 300 ብር እንደሚቆጥብ፣ ከጸሐፊነት ሥራው በተጨማሪ አስፈላጊ በሆነ ቦታ ሌሎቹን እንደሚያግዝ አጫውቶኛል፡፡ ወደ ማጣሪያው ጠጋ ብለን ስንመለከት የተለያዩ ሂደቶችን አስተዋልን፡፡ ስፖንጅ፣ የተለያየ መጠን ያላቸው ጠጠሮች፣ የተለያዩ በቱቦ የተገናኙ ፕላስቲክ ጋኖች ይታያሉ፡፡ አጠቃላይ የውሃ ማጣሪያ ዘዴው የአረቄ አወጣጥን (ዴስትሌሽን ሲስተምን) ይመስላል፡፡ ከዚህ በመነሳት ስለ ጠጠሮቹ ዓይነትና ከየት እንደተገኙ ጠየቅሁት። “ጠጠሮቹ River Gravel” ይባላሉ፡፡ የገፈርሳና የለገዳዲ ውሃ የሚጣራባቸው ናቸው፤ ብዙ ዓይነትና ደረጃ ቢኖራቸውም በመኪና እጥበቱ ስምንቱን ዓይነት ብቻ ነው የምንጠቀምባቸው” ብሏል፡፡

“የውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ሰሜን ቅርንጫፍ፣ እኛን ለማበረታታት በነፃ ነው የሰጡን” ያለው ስንታየሁ፤ እነዚያን ቁሶች በነፃ ባያገኙትና እንግዛ ቢሉ በጣም ውድ መሆኑንም ጠቁሞናል፡፡ አንዱ ካሬ ጠጠር ከ560 ብር በላይ ዋጋ ሲኖረው፣ ለውሃው ማጣሪያ ወደ 60 ካሬ ጠጠር ያስፈልጋል፡፡ ነገር ግን የውሃና ፍሳሽ ሰሜን ቅርንጫፍ ሃላፊዎች በስፍራው ተገኝተው ከጐበኟችው በኋላ፣ በሥራው በመደሰት ጠጠሮቹን በነፃ ሰጥተዋቸዋል፡፡ በዚህ ሥራ ውስጥ በርካታ ነገሮች አሉ፡፡ አካባቢን ከብክለትና ውሃን ከብክነት ይከላከላል፡፡ ደረጃውን የጠበቀ የመኪና እጥበትና ለበርካታ ወጣቶች የስራ እድል ማስገኘቱም ሌላው ጥቅም ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት አዲስ አበባ በብዙ የጽዳት ጉድለቶች የተጨናነቀች ከተማ መሆኗን የሚጠቅሰው ስንታየሁ፤ ጭንቀቷን ከሚጨምሩባት አንዱ የመንገድ ዳር የመኪና እጥበት እንደሆነ ይናገራል፡፡ በዚህም ዙሪያ ከፌደራል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ጋር በመነጋገር ውሃን በማጣራት መኪና ማጠብ ለሚፈልጉ ማህበራት ወይም ግለሰቦች ፕሮጀክቱን በነፃ ለመስጠትና በስፍራው እየተገኘ ሙያዊ ድጋፍ ለማድረግ ቃል መግባቱን ይናገራል፡፡ እስካሁን ቦሌ ክፍለ ከተማና አቃቂ አካባቢ ለሚገኙ ሁለት የመኪና እጥበት ማህበራት፣ ፕሮጀክቱን በነፃ ከመስጠቱም ባሻገር የምክር አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን አጫውቶኛል፡፡

ሪሳይክል እየተደረገ ጥቅም ላይ ስለሚውለው ውሃ ደህንነት ጥያቄ ባነሣሁ ጊዜ፣ አንዱን ሠራተኛ ጠርቶ በውሃው ፀጉሩን እንዲታጠብ አድርጐ ከማሳየቱም በላይ፣ ማኅበሩ ለ12 ጊዜ የውሃ ደህንነት ማረጋገጫ ያገኘበትን ሠርትፍኬቶች አሳይቶኛል፡፡ “ጉዳዩን ቀደም ሲል አስበንበታል፡፡ ለዚህም ፌደራል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን በየዓመቱ የውሃውን ናሙና እየፈተሸ ማረጋገጫ ይሰጠናል። 12ኛው ደብዳቤ (ማረጋገጫ) የ2005 ዓ.ም ፍተሻ የተደረገበት ነው” ሲል አስረዳኝ፡፡ “መጀመሪያ ውሃውን ስድስት ዙር በማጣራት እንጠቀም ነበር፡፡ አሁን ወደ ስምንት ዙር ከፍ አድርገን እየተጠቀምን ነው” ያለው ስንታየሁ፤ በቀጣይ 40 ዙር ሪሳይክል ለማድረግ አዲስ ፕሮጀክት እየቀረፁ ይገኛሉ፡፡ “በዚህ ዘርፍ ሌላ የሚፎካከረን ድርጅት ቢመጣ እኛ ወደተሻለ አዲስ ፕሮጀክት እናድግ ነበር” ብሏል፡፡ በቦታው የተባበሩት ፔትሮሊየም ምርቶችና ዕቃዎች በስፋት አይተን ጥያቄ አነሳን፡፡ ይህን ስራ ሲጀምሩ የተለያዩ ድጋፍ እንዲደረግላቸው በየማደያዎቹ ፕሮጀክቱን ቢያስገቡም ምላሽ የሚሰጥ ጠፋ፡፡

ተስፋ ሳይቆርጡ ወደተባበሩት ብሔራዊ ፔትሮሊየም ሄዱና ያልጠበቁትን ምላሽ አገኙ፡፡ እንደ ማህበሩ ሊቀመንበር ገለፃ፣ የተባበሩት ብሔራዊ ፔትሮሊየም ኩባንያ ኃላፊዎች ፕሮጀክቱን እንዳዩት ወደ ስፍራው በመምጣትና በመጐብኘት የካምቢዮ ዘይት ማጠጫ ማሽንን ጨምሮ 380 ሺህ ብር ግምት ያላቸው ዘመናዊ መሣሪያዎችን በነፃ እንደለገሷቸው ጠቅሶ፤ “አንዲህ አይነት ፈጣን ምላሽ ለሰጡን ወገኖች ከፍተኛ ምስጋናና አክብሮት አለን” ብሏል። ኩባንያው ዘመናዊ መሣሪያዎችን በነፃ ከመስጠት አልፎ እስከ መቶ ሺህ ብር የ“bp” የሞተር ዘይቶችን ሸጠን ትርፉን እንድንጠቀምና ዋናውን እንድንመልስ ሲሰጡን ምንም ማስያዣ አይጠይቁንም ይላል ስንታየሁ፡፡ በስፍራው ተገኝተን ለመረዳት እንደቻልነው “ይገርማል የመኪና እጥበት ድርጅት” ትልቅ ፕሮጀክት ነው፡፡ በቀን በትንሹ 120 መኪና በዛ ሲባል ደግሞ 180 መኪና ያጥባል፡፡ድርጅቱ በ10ሺህ ብር ካፒታል ሥራ የጀመረ ቢሆንም በአሁኑ ሠዓት ካፒታሉን ወደ 1 ሚሊዮን ብር ማሣደጉን ወጣት ስንታየሁ አየለ አስረድቶናል። ለወደፊት ትልቅ እቅድ አላቸው - እነዚህ መኪና አጣቢ ሠራተኞች፡፡ 54ቱን ሠራተኞች በእጥፍ በማሳደግ፣ 30 ደቂቃ ይፈጅ የነበረውን የአንድ መኪና እጥበት ወደ 15 ደቂቃ የማሳጠርና የደንበኞችን ጊዜ የመቆጠብ ሐሳብ አላቸው፡፡ “የትኛውም ነገር በገንዘብ ይገዛል፤ ጊዜን በገንዘብ ማግኘት አይቻልም፡፡ ስለዚህ ደንበኞችም እኛም ጊዜያችንን መጠቀም አለብን” ባይ ነው፤ ወጣት ስንታየሁ፡፡ ወጣቱ በመጨረሻም ለስራቸው መቀናት ትልቅ ድጋፍ ያደረጉ ድርጅቶችንና ግለሠቦችን አመስግኗል፡፡

በቅዱስ ጊዮርጊስ እና ኢትዮጵያ ቡና መካከል ከተደረገው የጥሎ ማለፍ ጨዋታ በፊት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች ይቅር ተባባሉ፡፡ ከወር በፊት የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች እና ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው አላግባብ በገቡት እሰጥ አገባ ተጠማምደው የነበረ ሲሆን ከትናንት በስቲያ በስታድዬም መላው ስፖርት አፍቃሪን ባስደሰተ ስፖርታዊ ጨዋነት ተታርቀዋል፡፡ በሌላ በኩል በኢትዮጵያ እግር ኳስ ከፍተኛ አስተዋፅኦ በማድረግ ከሚታወቁት ክለቦች ግንባር ቀደም ተጠቃሽ የሆነው የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ ነገ 36ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን በድምቀት ያከብራል፡፡የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ እና የክለቡ ደጋፊዎች ማህበር ‹‹የኢትዮጵያ ቡና በአዲስ ጎዳና›› በሚል መርህ ከኮንታክት መልቲ ሚድያ ጋር በመተባበር ሰፊ የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም እንዳዘጋጁ ታውቋል፡፡

ክለቡ በያዘው አዲስ አቅጣጫ ያለውን የደጋፊ ብዛት በመጠቀም በፕሮፌሽናል መንገድ በመደራጀት በስፋት ለመንቀሳቀስ ትኩረት እንዳደረገ ለማወቅ ተችሏል፡፡ኢትዮጵያ ቡና የተመሰረተው በ1975 ዓ/ም በቡና ቦርድ ስር ሆኖ ቡና ገበያ ስፖርት ክለብ በሚል ስያሜ ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜ ክለቡ የቡና ላኪዎች ማህበር ከምርት ገበያ ጋር በመሆን በጀት እየመደቡለት በቦርድ በመመራት እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ ለ36 ዓመታት በኢትዮጵያ የክለብ ውድድሮች በነበረው ተሳትፎ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሻምፒዮናነት አንድ ጊዜ ብቻ በ2003 ዓ.ም ሲያስመዘግብ ሌሎች የዋንጫ ድሎቹ 1 ጊዜ በኢትዮጵያ ሻምፒዮና 4 ጊዜ በኢትዮጵያ ጥሎ ማለፍ ሻምፒዮና ፤3 ጊዜ በኢትዮጵያ የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ እንዲሁም 1 ጊዜ የክለቦች ህብረት አሸናፊነት የተመዘገቡ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ ቡና በአራት የአፍሪካ ውድድሮች የመሳተፍ እድል ያገኘ ክለብ ሲሆን በኢትዮጵያ ጥሎ ማለፍ ውድድሮች በየጊዜው ሻምፒዮን የመሆን ልምድ አለው፡፡ ክለቡ ከዋናው ቡድን በተጨማሪ ተጠባባቂ የተስፋ ቡድን፤ በወጣት እና በሴቶች ቡድኖቹም እየሰራ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ በኢትዮጵያ እግር ኳስ የሚታወቀው ስታድየምን በማስዋብና በማድመቅ በሚታወቁት ደጋፊዎቹ ነው፡፡ የክለቡ ደጋፊዎች በአዲስ አበባ ስታድየም ቀኝ ጥላ ፎቅ፣ ካታንጋ እና ሚስማርተራ በብዛት ገብተው አስደናቂ የድጋፍ አሰጣጥ፤ ዝማሬ እና ህብረት በማሳየት የስፖርቱ አለኝታ ሆነው የቆዩ ናቸው፡፡

የሰውነትየምንግዜም ምርጥ አሰልጣኝነት? ለ3 አስርት ዓመታት በአህጉራዊ ውድድሮች አንቀላፍቶ የኖረውን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ወደ ተሳትፎ በማምጣት ውጤታማ በማድረግ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው አየተሳካላቸው ነው፡፡ የ61 ዓመቱ ሰውነት ቢሻው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ለአንድ አመት መንፈቅ ሲያሰለጥኑ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ እና ዋና ውድድር፤ በዓለም ዋንጫ ማጣርያዎች እና በወዳጅነት በድምሩ 12 ጨዋታዎችን በማድረግ ከ10 አገራት ብሄራዊ ቡድኖች ጋር ተጋጥመዋል፡፡ በውጤታቸውም 6 ድል፤ 4 አቻ እና ሁለት ሽንፈት አስመዝግበዋል፡፡ ከቤኒን እና ከሱዳን ብሄራዊ ቡድኖች ጋር 2 ጨዋታዎችን ሲያደርጉ ሌሎቹ አንድ አንድ ጊዜ የገጠሟቸው ብሄራዊ ቡድኖች ደግሞ ሶማሊያ፤ ደቡብ አፍሪካ፤ መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ፤ ቱኒዚያ ፤ዛምቢያ፤ቡርኪናፋሶ ፤ናይጄርያ እና ቦትስዋና ናቸው፡፡ ዘ ኢንስቲትዩት ኦፍ ፉትቦል ኮቺንግ የተባለ ተቋም ለዓለም አሰልጣኞች በሚያወጣው የብቃት ደረጃ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ባለፈው 1 ዓመት ተኩል ከነበሩበት የ350ኛ ደረጃ አሁን 120ኛ ላይ መድረሳቸውንም ያመለክታል፡፡

በትራንስፈርማርከት ድረገፅ ላይ በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ስኬት ላይ በተሰራ አሃዛዊ ስሌት መሰረት የአሰልጣኝነታቸው ስኬትም ድል በ33.33 በመቶ፤ አቻ በ41.67 በመቶ እንዲሁም ሽንፈት በ25 በመቶ በመቶ ተተምኗል፡፡ ከ31 ዓመት በፊት በሊቢያው የአፍሪካ ዋንጫ በመንግስቱ ወርቁ አሰልጣኝነት ከተሳተፈች በኋላ 17 ዋና አሰልጣኞች በብሔራዊ ቡድኑ ኃላፊነት የተፈራረቁ ሲሆን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ባለፈው 1 ዓመት ተኩል ባስመዘገቡት ውጤት የኢትዮጵያ እግር ኳስ የምንግዜም ውጤታማው አሰልጣኝ እየሆኑ መምጣታቸውን እያረጋገጡ ናቸው፡፡ ከ1 ዓመት ተኩል በፊት የቤልጄማዊው ቶም ሴንትፌይት ረዳት የነበሩት አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የብሄራዊ ቡድኑ ዋና አሰልጣኝ በመሆን መስራት የጀመሩት ለ2ኛ ጊዜ ነው፡፡

ከ2004 እሰከ 2006 እኤአ ብሄራዊ ቡድኑን በዋና አሰልጣኝነት ሲመሩ በ2005 እ.ኤ.አ በሩዋንዳ ላይ በዋና ብሔራዊ ቡድን እንዲሁም በ2004 እ.ኤ.አ ደግሞ አዲስ አበባ ላይ በወጣት ብሔራዊ ቡድን ሁለት የሴካፋ ዋንጫዎችን አሸንፈዋል፡፡ በ2001 እ.ኤ.አ ደግሞ በረዳት አሰልጣኝነት ከብሔራዊ ቡድኑ ጋር የሴካፋን ዋንጫ ማግኘትም ችለዋል፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ከ7 ዓመት በፊት በብሔራዊ ቡድኑ ሲሰሩ በ5 ዓመት ውስጥ 3 የሴካፋን ዋንጫ ማግኘታቸው ትልቅ ስኬት ነበር፡፡ በተጨማሪም አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የታዳጊ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆነው በመስራት ቦትስዋና ጋብሮኒ ላይ በተደረገ የአፍሪካ ታዳጊዎች ሻምፒዮና አራተኛ ደረጃ ለማግኘትም በቅተዋል፡፡ ባለፈው 1 ዓመት ተኩል ደግሞ ብሔራዊ ቡድኑን በኃላፊነት ይዘው ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ትንሳኤ የሚሆን ውጤት በማስመዝገብ እየተሳካላቸው ነው፡፡ የመጀመርያው ስኬታቸው ብሄራዊ ቡድኑ ከ31 ዓመታት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ እንዲያልፍ ማስቻላቸው ነው፡፡

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከ31 ዓመት በኋላ በአፍሪካ ዋንጫ ሲሳተፍ 3 ግጥሚያዎችን አድርጎ አንድ አቻ እና ሁለት ሽንፈት ፤ አንድ ጎል አግብቶ 7 ጎል ተቆጥሮበት ከምድቡ በጊዜ መሰናበቱ የሚታወስ ቢሆንም በውድድሩ ከፍተኛ አህጉራዊ ትኩረት ሊያገኝ የበቃ ነበር፡፡ በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የሚመራው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እያገኘ ባለው ስኬት ከፍተኛ የሽልማት ገንዘብ፤ በስፖንሰርሺፕ የገቢ ምንጭ በመፍጠር እና ደረጃውን በማሻሻልም ሆኖለታል፡፡ሼህ መሃመድ አልአሙዲ ለብሄራዊ ቡድኑ 5 ሚሊዮን ብር ከመሸለማቸውም በላይ የቡድኑ አብይ ስፖንሰር የሆነው በደሌ ቢራ በስፖንሰርሺፕ ውል ለ2 ዓመት እስከ 24 ሚሊዮን ብር በመክፈል ቡድኑን ማጠናከር ተችሏል፡፡ ኤምቲኤን የተባለ ኩባንያም በ6 ሚሊዮን ብር ብሄራዊ ቡድን ስፖንሰር ማድረጉም ይታወቃል፡፡ በአሁን ጊዜ በ50ሺ በር ወርሃዊ ደሞዛቸው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ውዱ ተከፋይ የሆኑት ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው 280 ሺ ብር የሚያወጣ ሊፋን መኪና በውጤታማነታቸው በማግኘትም ተጠቅመዋል፡፡

በአሰልጣኝ ሰውነት ሃላፊነት ዘመን በዋልያዎቹ ስብስብ ያሉ ተጨዋቾች በነፍስ ወከፍ በአማካይ 300ሺ ብር ለመሸለም እንደበቁም ይታወቃል፡፡ በሰውነት ቢሻው የሚመራው ብሄራዊ ቡድን ከአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ ባሻገር በ2014 እ.ኤ.አ ብራዚል ለምታስናግደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ ለማለፍ በሚደረገው የምድብ ማጣሪያም በተስፋ ሰጭ ውጤት በመጓዝ ላይ ይገኛል፡፡ በዓለም ዋንጫ ማጣርያው ደቡብ አፍሪካ፤ ቦትስዋና እና መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ የሚገኙበትን ምድብ የሰውነት ቢሻው ብሄራዊ ቡድን በ3 ጨዋታዎች ሰባት ነጥብ እና 3 የግብ ክፍያ በመያዝ እየመራ ነው፡፡

በብራዚል 2014 ላይ ለሚስተናገደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ የሚደረገው የምድብ ማጣሪያ በ4ኛ ዙር ሲቀጥል የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ሰኔ መጀመርያ ላይ ከቦትስዋና ጋር ከሜዳው ውጭ ይጋጠምና በሳምንቱ ደግሞ ከደቡብ አፍሪካ ጋር በአዲስ አበባ ይጫወታል፡፡ በዓመቱ መገባደጃ ላይ ደግሞ በመጨረሻው የማጣርያ ጨዋታ ከሜዳው ውጭ ከመካከለኛው አፍሪካ ጋር ይጋጠማል፡፡ ዋልያዎቹ በቀሪዎቹ 3 ጨዋታዎች ያለሽንፈት ከተጓዙ ከአንድ ብሄራዊ ቡድን ጋር በደርሶ መልስ የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ድልድል በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ለዓለም ዋንጫ የሚሳተፉበትን እድል ይወስናሉ፡፡ ይህን ማሳካት ደግሞ ለዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የምንግዜም ምርጥ አሰልጣኝነት ሁነኛ ማረጋገጫ ይሆናል፡፡

ሰር አሌክስ ፈርጉሰን ለ26 አመታት በከፍተኛ ስኬት አሰልጣኝ ሆነው ከሰሩበት ማንችስተር ዩናይትድ በ71 ዓመታቸው በጡረታ መሰናበታቸው ዓለም አቀፍ ትኩረት አግኝቷል፡፡ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች በህትመት፤ በኤሌክትሮኒክስ፤ በኢንተርኔት የመረጃ መረቦች እና ማህበራዊ ድረገፆች የፈርጊ ጡረታ መውጣት ከፍተኛ ሽፋን ተሰጥቶታል፡፡ በርካታ ዘገባዎች የዓለም እግር ኳስ እጅግ ታላቅ ባለሙያ ሳይታሰብ ማጣቱን፤ የፈርጊ ዘመን ማብቃቱን፤ እግር ኳስ የለወጡ እና ያሳደጉ መሆናቸውን በመጥቀስ ለሰር አሌክስ ፈርጉሰን ስንብት ሰፋፊ ሃተታዎችን በማቅረብ ዘክሯቸዋል።

ታላቁን የእግር ኳስ ጌታ ፈርጊ ለማስታወስ የሚከተሉትን 20 እውነታዎች ይመልከቱ፡፡ ስኮትላንዳዊ ዜግነት ያላቸው ሰር አሌክስ ፈርጉሰን በ6 የስኮትላንድ ክለቦች የአጥቂ መስመር ተጨዋችነት 317 ጨዋታዎች አድርገው 170 ጎሎች አስመዝግበዋል፡፡ ማን ዩናይትድን ከመያዛቸው በፊት በ3 የስኮትላንድ ክለቦች እና በስኮትላንድ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ሰርተዋል፡፡ በ1986 እኤአ ላይ ፈርጊ ማን ዩናይትድን በዋና አሰልጣኝነት ለመምራት ሲረከቡ የክለቡ የዋጋ ግምት 31 ሚሊዮን ዶላር የነበረ ሲሆን ከ26 አመታት በኋላ ክለቡን ሲለቁ ግን ክለቡ የዋጋ ግምቱ 3.2 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል፡፡

ክለቡን በ1986 እኤአ ላይ በሃላፊነት ሲረከቡ በየትኛውም ውድድር ለ19 ዓመታት ምንም አይነት ዋንጫ አላገኘም ነበር፡፡ ከ26 አመታት ስራ በኋላ በጡረታ ሲሰናበቱ ማን ዩናይትድ 39 ዋንጫዎችን ሰብስቧል፡፡ እነዚህ የዋንጫ ድሎች በትልልቅ የእንግሊዝ እና የአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ውድድሮች ሲመዘገቡ 13 በፕሪሚዬር ሊግ፤ 2 በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፤ 1 በፊፋ የዓለም ክለቦች ዋንጫ፤1 በአውሮፓ ካፕ ዊነርስ ካፕ፤ 1 በአውሮፓ ሱፕር ካፕ፤ 1 በኢንተርኮንትኔንታል ካፕ፤ 5 በኤፍ ኤ ካፕ እንዲሁም 10 በኮሚኒዊቲ ሺልድ የተገኙ ናቸው፡፡ ፈርጊ በማንችስተር ዩናይትድ እና ከዚያም በፊት በአሰልጣኝነት በሰሩባቸው ክለቦች በድምሩ 49 ዋንጫዎችን በማግኘት በእግር ኳስ ክለቦች የውድድር ታሪክ በዓለም አቀፍ ደረጃ በተለይ በመላው ብሪታኒያ ከፍተኛውን የስኬት ክብረወሰን አስመዝግበዋል፡፡ በፕሪሚዬር ሊግ የውድድር ታሪክ ፈርጊ ማን ዩናይትድን ለ26 አመታት ሲያሰለጥኑ በ44 ሌሎች ክለቦች 175 አሰልጣኞች ተፈራርቀው ሰርተዋል፡፡ እነዚህ 175 አሰልጣኞች በበተለያዩ ክለቦች በድምር በሰሩባቸውቨ 405 የውድድር ዘመናት 8 ጊዜ የሊጉን የሻምፒዮናነት ክብር ሲያገኙ ፈርጊ በ21 የውድድር ዘመናት 13 ጊዜ የፕሪሚዬር ሊግ ዋንጫን በማሸነፍ አስደናቂ ክብረወሰን አስመዝግበዋል፡፡

ፈርጊ በማን ዩናይትድ አሰልጣኝነት ከሰሩባቸው 9680 ቀናት በፊት አሁን በክለቡ የሚጫወቱ 17 ተጨዋቾች ገና አልተወለዱም ነበር፡፡ ከማን ዩናይትድ በጡረታ ሲሰናበቱ በእንግሊዝ እግር ኳስ አራት ዲቪዚዮኖች በሚወዳደሩ ክለቦች 1146 አሰልጣኞች ተፈራርቀዋል፡፡ ለ27 የውድድር ዘመናት በአንድ ክለብ አሰልጣኝነት በመስራት በሃላፊነት ለረጅም ጊዜ የቆዩ አሰልጣኞችን በአንደኛ ደረጃ ይመራሉ፡፡ በፈርጊ የሚሰለጥነው ማንችስተር ዩናይትድ በተለያዩ ውድድሮች ካደረጋቸው 1500 ጨዋታዎች 894 ድል ሲያደርግ ሽንፈት የገጠመው 267 ጊዜ ነው፡፡ በትራንስፈርማርከት ስሌት መሰረት ፈርጊ በአሰልጣኝነታቸው ያላቸው ስኬት እንደተመዘገበው 62.96 በመቶ ድል፤20.78 አቻ እንዲሁም 16.26 በመቶ ሽንፈት ነው፡፡

በእንግሊዝ ፕሪ ሚዬር ሊግ የተሳትፎ ታሪካቸው 2045 ነጥብ ሰብስበዋል፡፡ በፈርጊ ዘመን በአርሰናል፤ቼልሲ፤ ሊቨርፑል፤ ማን ሲቲ እና ቶትንሃም ክለቦች 51 አሰልጣኞች ተፈራርቀዋል፡፡ ፈርጊ ለ26 አመታት ማን ዩናይትድን ሲያሰለጥኑ ሪያል ማድሪድ 21፤ ኢንተር ሚላን 19፤ ቼልሲ 15፤ ባየር ሙኒክ 14፤ ጁቬንትስ 14፤ ማን ሲቲ 14፤ ኤሲ ሚላን 13 እንዲሁም ባርሴሎና 11 አሰልጣኞችን በሃላፊነት መንበር አፈራርቀዋል፡፡ በሙሉ ቡድኑ 29 ተጨዋቾች እና 15 ከእንግሊዝ ውጭ ዜግነት ያላቸው ያሰባሰበው የፈርጊ ማንዩናይትድ ቡድን በትራንስፈርማርከት ያገኘው የዋጋ ተመን 370 ሚሊዮን ፓውንድ ነው፡፡ የቡድኑ አማካይ እድሜ 27.5 አመት ሲሆን የአንድ ተጨዋች አማካይ ዋጋ 14.36 ሚሊዮን ፓውንድ ነው፡፡ በክለቡ የ26 ዓመታት ቆይታቸው 104 ተጨዋቾችን በግዢ ኦልድትራፎርድ ያመጡት ፈርጊ በክለቡ ባፈሯቸውና ዘ ፈርጊ ቤቢስ በተባሉ ምርጥ ተጨዋቾቻውም ይታወሳሉ፡፡

የፈርጊ ውጤት የሆኑት እውቆቹ ተጨዋቾች ራያን ጊጊስ፤ ፖል ስኮልስ፤ ዴቪድ ቤካም፤ ጋሪ ኔቭል፤ ኒኪ በት እና ዌልቤክ ይጠቀሳሉ፡፡ ፈርጊ በተጨዋቾች ግዢ በ26 ዓመታት ውስጥ 546.5 ሚሊዮን ፓውንድ ሲያወጡ በሽያጭ ደግሞ 226.5 ሚሊዮን ፓውንድ ገቢ አድርገዋል፡፡ በማንችስተር ዩናይትድ ዋና አሰልጣኝነት ከ26 ዓመት በፊት ሲቀጠሩ የዓመት ደሞዛቸው 60ሺ ፓውንድ ነበር፡፡ በ2013 እኤአ በዓመታዊ ደሞዝ 7 ሚሊዮን ፓውንድ የሚታሰብላቸው ፈርጊ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ የዘንድሮ ሻምፒዮናነት ባገኙ ማግስት በሰንደይ ታይምስ ተሰርቶ በወጣ የእንግሊዝ እግርኳስ ሃብታሞች ዓመታዊ ደረጃ በ34 ሚሊዮን ፓውንድ ሃብት አንደኛ ናቸው፡፡ ፈርጊ እግር ኳስን በቲቪ የመመልከት ልማድ ያላቸው ሲሆን በምእራቡ ዓለም የተሰሩ የጦርነት ፊልሞችን መመልከትም ያዘወትራሉ፡፡ ክላርኔት የተባለ ሙዚቃ መሳርያ መጫወትም ይችላሉ፡፡

ፈርጊ ጡረታቸውን ባሳወቁ በኢንተርኔት የማህበረሰብ ድረገፆች ከፍተኛ ትኩረት ስበው ነበር፡፡ ጡረታቸው በታወጀ 24 ሰዓት ውስጥ በጉዳዩ ላይ 6 ሚሊዮን የቲውተር መልክቶች ተሰራጭተዋል፡፡ ፈርጊን ለመተካት ጡረታ በወጡበት ማግስት የኤቨርተኑ ዴቭድ ሞየስ ቅድሚያ ግምት ቢወስድም፤ በሪያል ማድሪድ ያሉት ጆሴ ሞውሪንሆና የጀርመኑ ክለብ ዶርትመንድ አሰልጣኝ ጀርገን ክሎፕ በእጩነት ተጠቅሰዋል፡፡ ከእነዚህ አሰልጣኞች ባሻገር በምትክነት የታጩት በፈርጊ የሰለጠኑትና ከፈርጊ ቤቢስ አባላት መካከል የሆኑት የቀድሞ ተጨዋቾች ራያን ጊግስ፤ ኦሌ ጉናር ሶልሽየር እና ፖል ስኮልስ ነበሩ፡፡ ፈርጊ እንዲተካቸው የሚፈልጉት ራያን ጊጊስ እንደሆነ ተናግውም ነበር፡፡ በመጨረሻም ምትኩ ዴቪድ ሞይስ ሆኗል፡፡ በኤቨርተን ክለብ ለ11 ዓመት ያሰለጠነው ዴቪድ ሞዬስ የማን ዩናይትድ ቦርድ በሙሉ ድምፅ የፈርጊ ምትክ አድርጎ እንዲሰራ በመምረጥ የ6 ዓመት ኮንትራት ሰጥቶታል፡፡ የ50 ዓመቱ ዴቪድ ሞይስ በማን ዩናይትድ አሰልጣኝነት መስራት ሲጀምር በሳምንት 80 ሺ በዓመት 4 ሚሊዮን ፓውንድ ይከፈለዋል፡፡

መጋቢት 29 ቀን 2005 ዓ.ም ማለዳ እንግዶች ለመቀበል ቦሌ አለም አቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ ነበርኩ፡፡ ግልፅ ባልሆነ ምክንያት እንግዶችን የሚቀበሉም ሆነ የሚሸኙ ሰዎች የሚገቡበት በር አልተከፈተም ነበርና ውጭ ለመቆም ተገደድኩ፡፡ ብዙ አውሮፕላኖች ስለአረፉ ተጓዦች፣ ሆስተሶችና ፓይለቶች ወደ ውጭ ይጎርፋሉ፡፡ ሆስተሶቹና አንዳንድ ፓይለቶች ቆመው ወደቤታቸው የሚወስዳቸውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ መኪና ይጠባበቃሉ፡፡ የሚጠብቁት መኪና ማቆሚያ ቦታ ላይ ሆነው ነው፡፡ ምንም መቀመጫ ስላልነበረም አንዳንዶቹ ሆስተሶች ሻንጣቸው ላይ ተቀምጠው አየሁ፡፡ ነገሩን ለመቀበል ስላዳገተኝ በሞባይሌ ጥቂት ፎቶዎች አነሳሁ፡፡

እነዚህ ሆስተሶች እዚህ የደረሱት ቢያንስ ከአራት ሰአት በረራ በኋላ ነው፡፡ ከዚያ በፊትም ዝግጅት ማድረግ ስለሚኖርባቸው ሌሊቱን ሳይተኙ ነው የመጡት ማለት ነው፡፡ በበረራው ጊዜም አንድ አውሮፕላን ህዝብ ሲንከባከቡ እንዳደሩ ግልጽ ነው፡፡ እንደኔ ግምት እነዚህ ሰዎች በዚያ ጠዋት የሚመኙት ዋና ነገር ቢኖር ወደቤታቸው ቶሎ ሄደው መተኛት ነው፡፡ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቢቻል እንደመጡ የሚወስዳቸው መኪና፣ባይቻል ደግሞ ከነክብራቸው የሚቆዩበት ማረፊያ ቦታ ማዘጋጀት ለምን ተሳነው? ነገሩን መቀበል ያቃተኝ እኔ ብቻ አልነበርኩም፡፡ አንድ ከፊቴ የቆመ ሰው “እስቲ አሁን ዝናብ ቢኖር እንዴት ነው እዚህ ሆነው የሚጠበቁት?” አለ፡፡

ሌላው ያስገረመኝ ነገር ደግሞ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሆስተሶቹንና ፓይለቶቹን ለማጓጓዝ የሚጠቀምበት ብዙ ዓመታት ያገለገሉ መኪኖችን ነው፡፡ እቃ መጫኛ ስለሌለው ሻንጣም ሰውም አብሮ ነው የሚጫነው፡፡ አንድ ከሻንጣ ጋር የተጫነ ፓይለት እያየሁ እንዲህ ስል አሰብኩ “በመቶዎች የሚቆጠር ሰዎችን በጥንቃቄ ሲያበር ያደረን ሰው እንዲህ መጫን ምን ይባላል?” ስንት ከባድ ነገሮችን አቅዶ ለሚያሳካው አየር መንገድ ምክር ካስፈለገው ከኋላቸው የሚከፈቱ ሚኒባሶች ቢኖሩት ሰዎቹ ከፊት ከነክብራቸው ሲቀመጡ፣ ሻንጣዎች ከኋላ እንዲሆኑ ማድረግ ይቻል ይሆናል፡፡ አየር መንገዱን የላቀ አየር መንገድ ለማድረግ፣ለሠራተኞቹ አያያዝ ትኩረት መስጠት እንደሚገባው ባስታውሰው ከአጉል ድፍረት እንደማይቆጠርብኝ በመተማመን ነው፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

ተጨማሪ የሙስና ተጠርጣሪዎች ዛሬ እንደሚታሰሩ ምንጮች ተናግረዋል

የጉምሩክና ገቢዎች ባለሥልጣን ዋና ዳሬክተር አቶ መላኩ ፈንቴና ምክትል ዳሬክተሩ አቶ ገብረዋህድ ወ/ጊዮርጊስ፣ እንዲሁም የ“ኬኬ” ኩባንያ ባለቤት አቶ ከተማ ከበደን ጨምሮ አስራ ሁለት ግለሰቦች በሙስና ተጠርጥረው አርብ ዕለት በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ዋሉ፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ባለሥልጣናትና ባለሃብቶች አርብ ጠዋት ከያሉበት በፖሊስ ተይዘው እንደተወሰዱ የገለፁ ምንጮች፤የቤት ብርበራ ሲካሄድ ማምሸቱንም ተናግረዋል፡፡ የፀረሙስና ኮሚሽን ማታ ሁለት ሰዓት ላይ በኢቴቪ በሰጠው መግለጫ፤ የጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳሬክተርና የሚኒስትሮች ካቢኔ አባል አቶ መላኩ ፈንቴ እና ምክትል ዳሬክተር አቶ ገብረዋህድ ወ/ጊዮርጊስ በሙስና ተጠርጥረው እንደታሰሩ ተገልጿል፡፡ ከሁለቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት በተጨማሪ ባለሃብቶችም በቁጥጥር ስር እንደዋሉ ኮሚሽኑ ገልፆ፤ ከብሔራዊ የመረጃና ደህንነት ጋር በመተባበር ምርመራ ማካሄዱን ተናግሯል፡፡

ከበርካታ ባለሃብቶችና ነዋሪዎች የቀረቡ አቤቱታዎችና ጥቆማዎች ለምርመራው እንዳገዙት ኮሚሽኑ ጠቅሶ፤ ተጠርጣሪዎቹን ወደ ፍ/ቤት በማቅረብ ክስ እመሰርታለሁ ቢልም ዝርዝር መረጃ አልሰጠም፡፡ በአገሪቱ አሉ ከሚባሉት ባለሃብቶች መካከል የሚጠቀሱት አቶ ከተማ ከበደ፤ ተጠርጥረው ከታሰሩት ባለሃብቶች አንዱ ሲሆኑ በበርካታ የኢንዱስትሪና የንግድ መስኮች የተሰማራው “ኬኬ” ኩባንያ ባለቤት ናቸው፡፡ ከ20 ዓመት በፊት የተመሠረተው “ኬኬ” ኩባንያ፤ አጀማመሩ ከትንሽ ደረጃ ላይ የተነሳ ስለነበር ሥራው የሚመራውና አብዛኛው ሥራ የሚከናወነው በድርጅቱ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ ከተማ ከበደ እንደነበር የድርጅቱ ይፋዊ መረጃ ይገልፃል፡፡

በልብስና በቀለም ምርት የተሰማራው “ኬኬ”፤ የከባድ ማሽነሪዎች አስመጪ በመሆንም በስፋት ይታወቃል፡፡ ከጊዜ በኋላም በቡና ኤክስፖርት እንዲሁም በእርሻ ኤክስፖርትና በማዳበርያና ተባይ ማጥፊያ ምርቶች አስመጪነት በመሰማራት ሥራውን እንዳስፋፋ የድርጅቱ መረጃ ይዘረዝራል፡፡ የሚኒስትሮች ካቢኔ የሆኑት አቶ መላኩ ፈንቴ ከሥልጣናቸው ይነሳሉ ተብለው ለወራት ሲወራ የነበረ ሲሆን ምክትላቸው አቶ ገብረዋህድ ደግሞ ባለፈው የካቲት ወር በፓርቲው ውስጥ ከነበራቸው ሃላፊነት መነሳታቸው ይታወሳል፡፡ በተያያዘ ዜና፣ አርብ እለት ከተፈፀመው እስር እንዲሁም ሌሊቱን ሙሉ ከተካሄደው የተጠርጣሪዎች ቤት ብርበራ በተጨማሪ፣ ዛሬ ቅዳሜ እለትና በቀጣዮቹ ቀናት በቁጥጥር ስር የሚውሉ ሎሎች ተጠርጣሪዎች እንደሚኖሩ ምንጮች ጠቁመዋል።

Published in ዜና

በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ኢትዮጵያን በመወከል እስከ 2ኛ ዙር ማጣርያ የመልስ ጨዋታ ተጉዞ በግብፁ ክለብ ዛማሌክ የተሸነፈው ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ኮንፌደሬሽን ካፕ ጥሎ ማለፍ ተሸጋግሮ ከሌላው የግብፅ ክለብ ኢኤንፒፒአይ ጋር ተደለደለ፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ውጭ የሆነው ከሳምንት በፊት ከግብፁ ዛማዜክ ጋር አዲስ አበባ ላይ የመልስ ጨዋታውን አድርጎ 2-2 አቻ በመለያየቱ ነው፡፡ ሁለቱ ክለቦች በሻምፒዮንስ ሊጉ የሁለተኛ ዙር ማጣርያ የደርሶ መልስ ጨዋታ በአጠቃላይ ውጤት 3ለ3 ቢሆኑም ዛማሌክ ወደምድብ ድልድል የገባው ከሜዳ ውጪ ብዙ ባገባ በሚለው ህግ ነው፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ሻምፒዮንስ ሊጉ የምድብ ድልድል ለመግባት ሳይችል ቢቀርም በውድድር ዘመኑ በአፍሪካ የክለብ ውድድር ያለውን ተሳትፎ ቀጥሏል፡፡

በኮንፌደሬሽን ካፕ ጥሎ ማለፍ 16 ክለቦች የሚሳተፉ ሲሆን የመጀመርያው ዙር ግጥሚያዎች ከሳምንት በኋላ ይካሄዳሉ፡፡ ጊዮርጊስ ከግብፁ ክለብ ጋር በኮንፌደሬሽን ካፑ ጥሎ ማለፍ የመጀመርያ ጨዋታውን የዛሬ ሳምንት በሜዳው ያደርጋል፡፡ በሌሎች ጨዋታዎች የማሊው ስታድ ዴማሊ ከብሩንዲው ኤልኤል አካዳሚ፤ የናይጄርያው ኢኑጊ ሬንጀርስ ከ ቱኒዚያው ሳፋክሲዬን፤ የሞሮኮው ኢፍዩኤስ ራባት ከሌላው የሞሮኮ ክለብ ኤኤስኤፍ ራባት፤ የቱኒዚያው ቤዘርቲን ከግብፁ ኢስማኢሊያ፤ የአልጄርያው ሴቲፍ ከጋቦኑ ዩኤስ ቢታም እንዲሁም የዲሞክራቲክ ኮንጎው ቲፒ ማዜምቤ ከሞዛምቢኩ ሊጋ ሙኩሉማና ይገናኛሉ፡፡

ጊዮርጊስ ከግብፁ ክለብ ኢኤንፒፒአይ ጋር በአፍሪካ ደረጃ ሲገናኝ ለሁለተኛ ጊዜ ነው፡፡ ሁለቱ ክለቦች በ2006 እኤአ ላይ በሻምፒዮንስ ሊግ የመጀመርያ ዙር ተገናኝተው ነበር፡፡ በወቅቱ የመጀመርያው ጨዋታ ካይሮ ላይ ሲደረግ ያለምን ግብ አቻ የተለያዩ ቢሆንም በመልሱ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ በሜዳው ኢኤንፒፒአይን 1ለ0 አሸንፎ ወደ ሁለተኛ ዙር ለመሸጋገር እንደበቃ ይታወሳል፡፡2 የውጭ ፕሮፌሽናሎችን ጨምሮ 27 ተጨዋቾችን በስብስቡ የያዘው የግብፁ ክለብ ኢኤንፒፒአይ በ48 ዓመቱ ግብፃዊ ታሬክ ኤልአሽሪ ዋና አሰልጣኝነት የሚመራ ነው፡፡

የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ፓርቲ ዋና ጸሐፊ በመሆን ለአስር አመታት ያገለገለው አቶ ማሙሸት አማረ “በፓርቲው ህልውና ላይ ጉዳት አድርሰሀል” በመባል እሱን ጨምሮ 17 የፓርቲው አመራሮች ከፓርቲው የታገዱት የዛሬ ሁለት ዓመት ገደማ ነው፡፡ ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት በመውሰድ ሲከራከሩ የነበሩት እነ ማሙሸት አማረ እና እነ ኢንጂነር ሃይሉ ሻውል ሲሆኑ ፍ/ቤቱም ተከሳሽ የነበሩ እነ ማሙሸት “ምንም አይነት ሁከት አልፈጠሩም” በማለት ወደ ፓርቲው እንዲመለሱ መስጠቱ ይታወሳል። ሆናም ትዕዛዙ ተግባራዊ ሳይሆን አንድ ዓመት አልፎታል፡፡ “ፓርቲው ውስጣዊ ችግሮች አሉበት” በማለት የሚናገሩት እነ አቶ ማሙሸት፤ ዛሬ የፓርቲውን ችግር በውይይት ለመፍታትና “ጠቅላላ ጉባኤ ይጠራ” በማለት ከምርጫ ቦርድና ከኢንጂነር ኃይሉ ሻውል ጋር እየተነጋገሩ ነው፡፡ ጋዜጠኛ ሰላም ገረመው በእነዚህ ጉዳዮች ዙሪያ አቶ ማሙሸት አማረን አነጋግራለች፡፡

ከመኢአድ ከታገድክ ስንት ጊዜ ሆነህ?

በ2003 ዓ.ም በተደረገ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ነው የዚህ ፓርቲ ዋና ፀሐፊ በመሆን የተመረጥኩት። ከዚያ በኋላ ነው የታገድኩት፡፡ በአቶ ሃይሉና በአቶ ያዕቆብ ከፓርቲው ውጪ በሄደ ደንብ የውስጥ አለመግባባት ተፈጥሮ አቶ ኃይሉ ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት ወስዶ ክርክር ከተደረገበት በኋላ ፍ/ቤቱ የተከሰስንበት ጉዳይ ስህተት መሆኑን አውቆ ወደ ፓርቲያችን እንድንመለስና ጠቅላላ ጉባኤው ተሰብስቦ የመጨረሻ እልባት እንዲሰጥ ተወሰነ፡፡ ከሳሾች ፍ/ቤቱ ትክክል አልፈረደም ብለው ለከፍተኛ ፍ/ቤት ይግባኝ ጠይቀው ነበር፡፡ ሆኖም ፍ/ቤቱ የስር ፍ/ቤትን ውሳኔ አጸና፡፡ አቶ ሀይሉና ሌሎቹ ግን የችሎቱን ትዕዛዝ ማክበር ባለመቻላቸው፣ ምርጫ ቦርድ ውሳኔውን እንዲያስፈጽም ትዕዛዝ ሰጠልኝ፡፡ ቦርዱም ይህንን መነሻ በማድረግ ለአቶ ሃይሉ በ2004 ዓ.ም ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠሩ ትዕዛዝ ቢሰጥም ጉባኤው ሳይጠራ ቀረ፡፡ እኛም ትግላችንን በህጋዊ መንገድ በመቀጠል ያላሰለሰ ጥረት አደረግን፡፡ ይኼም ተቀባይነት ሊያገኝ አልቻለም፡፡ እንግዲህ እንደምንሰማው አቶ ሃይሉ “አባረናል አጥርተናል” ይላሉ፡፡ ሆኖም እሳቸው የማባረርም የማጽዳትም ስልጣን የላቸውም፡፡

የመኢአድ አባል ስትሆን ምኑን መርጠህ ነው?

ከ1984 ሚያዚያ 15 ጀምሮ መ.አ.ህ.ድ ነበርኩ። ኢህአዴግ ከገባ በኋላ በአማራው ተወላጅ ላይ በየክልሉ ከፍተኛ በደል ሲያደርግ ይሄ በደል ይቁም በማለት በዚህ እንቅስቃሴ ለመሳተፍ ነው አባል የሆንኩት፡፡ ከዚህ በኋላ የታገልንለት ህዝብ ለምን ለአማራው ብቻ ትታገላለችሁ ሁሉም ብሔሮች ችግር እየደረሰባቸው ነው ያሉት፤ ለምን ለሁሉም ብሔር አትታገሉም የሚል ከፍተኛ አስተያየት በመኖሩ አባላቱ በሰጡት ውሳኔ መሠረት በ1995 ዓ.ም መአህድ ወደ መኢአድ ተቀየረ፡፡ መአህድ ወደ መኢአድ ከተቀየረ 10 አመት ሆኖታል፡፡ በዚህ ጊዜ የፕሬዚዳንቱን ችግር አታውቁም ነበር? በዚህ ፓርቲ ውስጥ በርካታ ችግሮች ይታዩ ነበር፡፡ ነገር ግን የሚፈቱት በውይይት ነበር፡፡ አንድ ሰው ችግር አለበት ተብሎ ከታሰበ ውይይት ላይ ይቀርባል፡፡ ያ ውይይት የቀረበበት አጀንዳ፣ የፓርቲው ስራ አስፈፃሚ በጊዜያዊነት ያግድና ለላዕላይ ምክር ቤት ያቀርባል፡፡ ም/ቤቱም ያይና የመጨረሻ ውሳኔ በመስጠት በጠቅላላ ጉባኤ ላይ ያሳውቃል፡፡ የእኛ መታገድ ግን ከዚህ የተለየ ነበር፤ በፕሬዚዳንቱ ደብዳቤ ብቻ ነው “ሁከት ፈጥራችኋል” ተብለን ወደ ፍ/ቤት የሄድነው መጀመሪያም ወደ ፍ/ቤት የሄድነው ያለ አግባብና ከመተዳደሪያ ደንቡ ውጪ ነው፡፡ በመተዳደሪያ ደንቡ መሠረት ሄደው ሳይሳካ ሲቀር ነው ፍ/ቤት የሚኬደው፡፡ ሌሎች በህገደንቡ መሠረት ከፓርቲው ከታገዱና ከተሰናበቱ ለምን እናንተ በህገወጥ መንገድ ሆነ ትላላችሁ?

እኛ ያቀረብነው መከራከሪያ ሃሳብ ትክክለኛ መረጃ ይዘን ነው፡፡ ለምሳሌ ከታህሳስ 15-17 2003 ዓ.ም በተካሄደ ጠቅላላ ጉባኤ፣ አቶ ሃይሉ አቶ ያዕቆብን ከመተዳደሪያ ደንቡ ውጭ ተቀዳሚ ሊቀመንበር አድርጌ ሾሜዎአለሁ አሉ፤ እሳቸው ይህንን ማድረግ አይችሉም፡፡ እሳቸው የሚችሉት ከሌላ ስራ አስፈፃሚዎች ጋር ሆነው ሌላ ስራ አስፈፃሚ የሚሆኑትን በመምረጥ ለላይዕላይ ም/ቤት ያቀርባሉ፤ ላዕላይ ም/ቤቱ ነው የሚያፀድቀው፡፡ ይኸ ሹመት ነው፡፡ በሊበራል ስርዓት በአንድ ግለሰብ የሚመረጥ ሹመት የሚባል ነገር የለም፡፡ በምርጫ ነው የሚደረገው፤ ባላቸው የስራ ልምድና የትምህርት ሁኔታ ነው፡፡ በዚህ ከተመረጠ ያልፋል፡፡ ካልተመረጠ ይወድቃል፡፡ እሳቸው ግን ቀጥታ አምጥተው አቶ ያዕቆብን ተቀዳሚ ሊቀመንበር አድርገው ሾሙ፡፡ ይሄ ነው ችግሩ፡፡ አንደኛ አቶ ያዕቆብ የድርጅቱ አባል አልነበሩም፡፡ የዕለቱ ዕለት ነው ለላዕላይ ም/ቤት ቀርቦ አባል ነው የተባለው፤ ዛሬ አባልነቱ ቀርቦ ወዲያውኑ ፕሬዚዳንት የሚሆንበትን ስርዓት ደንባችን አይፈቅድም፡፡ ይሄ ታዲያ በአቶ ሃይሉ ዘንድ እንደቂም ተወሰደ፡፡ እንዴት እኔ የምለውን አያከብሩም ብለው ተቆጡ፡፡ እኛ ደግሞ ማንም ከመተዳደሪያ ደንባችን ውጭ ከሆነ ስለምንታገል፤ ዋና አላማችንም ይሄ ስለሆነ እስከ መጨረሻው ፀንተናል፡፡ አቶ ሃይሉ አንድ አባልን ማገድ እንኳን የሚችሉት ለሁለት ወር ጊዜ ብቻ ነው፡፡ እኛ ደግሞ አመራሮች ነን፤ በእሳቸው ልንታገድ አንችልም፡፡ ወሳኙ ደግሞ ጠቅላላ ጉባኤው ነው፡፡ ከ105 የላዕላይ ም/ቤት ውስጥ በተለያዩ ችግሮች 82 ሲቀሩ፣ ከነዚህ ውስጥ 57 የሚሆኑት አባላት ከእኛ ጋር ናቸው፡፡ ስለዚህ ይሄንን ሃሳባቸውን ለም/ቤቱ አቅርበው የሚያፀድቅላቸው ስለሌለ ነው አኩርፈው የተቀመጡት፡፡ አሁንም ለመነጋገር የማይፈልጉትም ለዚህ ነው፡፡ አሁንም “በውይይት እንፍታ ሲባሉ አልፈልግም” ያሉት ለዚህ ነው፡፡ የተቃወምነውን ትክክል ነው ብለን ሲቃወሙን ከቆዩ በኋላ አቶ ያዕቆብን በደብዳቤ አባረዋል፡፡ እናንተ በፓርቲው ውስጥ አመራር በነበራችሁ ጊዜ የኢንጂነር ኃይሉ ተቀናቃኞች ኢንጂነሩ ስልጣናቸውን ይልቀቁ ይሉዋችሁ ነበር፡፡

እናንተ ይሄን ችግር በወቅቱ አታውቁም ነበር?

ሌሎች ከፓርቲው ወጥተው ነገሩን ይተውታል አሊያም ሌላ ፓርቲ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ቅልውጥና ነው፤ ሌላ ነገር አይደለም፤ ማንም የፖለቲካ ሰው ላሰበበት ዓላማ መሳካት እስከመጨረሻው መታገል አለበት፡፡ አንድም አባል ግን እኛን ይሄንን ችግር አደረሳችሁብኝ ብሎ አጀንዳ ያስያዘ የለም፡፡ የመጀመሪያው እኔ ነኝ፡፡ እኛን ብዙ ጊዜ ሲሰድቡን አውቃለሁ፡፡ እኔ ግን ለግለሰብ አጐብድጄአለሁ፡፡ በፍፁም ሌሎቹ በጭቆና አይደለም የሚወጡት፡፡ እኛ ብቻ ነን በጭቆና የታገድነው፤ ስለዚህ እስከዚያ ድረስ በፓርቲው ውስጥ ትልቅ ችግር የሚባል አልነበረም፡፡ የእናንተ ቅሬታ ኢንጂነር ኃይሉ አቶ ያዕቆብን በመሾማቸው ነው፡፡

ኢንጂነር ሃይሉ እንዲመረጡ ደግሞ አንተ በአባላቱ ላይ ግፊት አድርገሃል፡፡ ታዲያ አሁን ለምን ችግር አለ ትላለህ?

በመጀመሪያ አቶ ያዕቆብ በምርጫ ባለመመረጣቸው ነው ቅሬታ ያቀረብነው፡፡ አቶ ያዕቆብን ያመጡዋቸውም አቶ ሃይሉ ናቸው፡፡ ይሄ ስንቃወም ስልጣን ፈልጋችሁ ነው ተብለናል፡፡ ከ400 በላይ ለሆኑ የጠቅላላ ጉባኤ አባላት አቶ ሃይሉን ምረጡ ብዬ የቀሰቀስኩት እኔ ነኝ፡፡ በዛን ሰአት እኔን ምረጡኝ ማለት እችል ነበር፡፡

ለምን ኢንጂነር ሃይሉ እንዲመረጡ አደረግህ?

ፓርቲው ላይ ትንሽ ችግር ነበር፡፡ አቶ ሃይሉ ለስምንት ወራት ከ2002 ምርጫ በኋላ ወደ ፓርቲው አልመጡም፡፡ ለዶ/ር ታዲዮስ ውክልና ሰጥተው ነበር የሚፈረመው፡፡ ጠቅላላው ጉባኤው ይጠራ ብለን ወጥረን ስንይዝ፣ አቶ ያዕቆብ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ አልፈለጉም፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ጠቅላላ ጉባኤው አቶ ያዕቆብን አያውቃቸውም፡፡ በዚህ መሃል አቶ ኃይሉ ወደ ቢሮ እንዲመለሱ አቶ ያዕቆብ ግፊት እያደረጉ ነበር፡፡ አንተ ለአባላቱ ከነገርክልኝ ልመረጥ እችላለሁ ማለታቸውን ያወቅነው ከጠ/ጉባኤ አባላቱ ሲወጡ “እንዲህ እየተባልን ነው፤ አቶ ሃይሉ ደውለው አቶ ያዕቆብን ምረጡ እያሉን ነው” የሚል ነገር ነገሩን፡፡ የላዕላይ ም/ቤቱ የሚያቀርብላችሁን ሰው እጃችሁን አውጥታችሁ ስትመርጡ ነው እንጂ በጐን እየተደወለ ምረጡ ስለተባላችሁ ብትመርጡ አይሆንም አልን፡፡ ስለዚህ እንደዚህ አይነት ችግር ከመጣ ሠላማዊ ሽግግር ስለሚያስፈልግ ተብሎ አቶ ሃይሉ ይሄንን ፓርቲ ለስድስት ወር መምራት አለባቸው በሚል የጠቅላላ ጉባኤውን አባላት ምርጫችሁ ኢንጂነር ሃይሉ መሆን አለበት ብያቸው ነበር፡፡ ሁሉም በደስታ ተቀብለው የተባሉትን አደረጉ፡፡ እሳቸውም መድረክ ላይ ወጡና ደከመኝ ስል አልሰማም ብላችሁ እኔን መርጣችኋል፤ ስለዚህ እኔን እንዲያግዙኝ አቶ ያዕቆብ ልኬን ወክያለሁ ሲሉ ችግር ተፈጠረ፡፡

ችግር የፈጠሩት ኢንጂነር ሃይሉ ናቸው እያላችሁ ነው፤ ቀድማችሁ አቶ ያዕቆብን ምረጡ ማለታቸውንም ታውቃላችሁ፡፡ ይሄንን እያወቃችሁ ለምን እንዲመረጡ ፈለጋችሁ?

ጠቅላላ ጉባኤ የምንጠራበት ጊዜ ሊያልፍብን በመሆኑ ሳያልፍ ነበር ለማካሄድ ያስፈለገው። በወቅቱ ደግሞ ለፕሬዚዳንትነት የተሾመ ሰው አልነበረም፡፡ ስለዚህ አቶ ሃይሉን ስንመርጥ በህመምና በመሰልቸት ምክንያት ቤታቸው ቀሩ ብለን አስበን እንጂ እንዲህ አይነት ተንኮል ለማድረግ አስበዋል ብለን አልገመትንም። ይሄንንም የሰማነው አባላቱ ተጠቃለው አዲስ አበባ ከገቡ በኋላ ነው፡፡ ችግር እየፈጠሩ መሆናቸውን የሰማኸው ጠቅላላ ጉባኤው ሊካሄድ ሁለት ቀን ሲቀረው ነው ብለሃል። ነገር ግን ችግሩን ከመፍታት ይልቅ መልሳችሁ እሳቸውን መርጣችኋል፡፡ አሁን ደግሞ ችግር ፈጠሩ እያላችሁ ነው፡፡ ሌሎች ደግሞ ማሙሸት እራሱን በአቶ ያዕቆብ ቦታ ለመተካት አስቦ ስለነበር ነው ይላሉ… ይሄ ከእውነት የራቀ የሞኞች ሃሳብ ነው። እኔ የስልጣን ጥም የለብኝም፡፡ ብፈልግ ደግሞ እኔ እራሴን አስመርጥ ነበር እንጂ አቶ ሃይሉን አላስመርጥም ነበር። ይሄንን ለማድረግ ለእኔ ቀላል ነው፡፡

አቶ ያዕቆብ ለጠቅላላ ጉባኤ ምርጫ በዕጩነት ባለመቅረባቸው ነው ችግራችሁ ወይስ ሙሉ በሙሉ ለዕጩነት መቅረብ አይችሉም ነው ተቃውሟችሁ?

አቶ ያዕቆብ አይደለም ለአመራርነት ለፓርቲ አባልነትም አይበቁም፡፡ በጣም ችኩል ናቸው። የቆዩትም በብዙ ችግር ነው፡፡ አቶ ያዕቆብ የፓርቲ አባል ሆነው አያውቁም፡፡ ዛሬ ጠዋት የመኢአድ የላይላይ ም/ቤት አባል ሆነው፣ ነገ ደግሞ ስራ አስፈፃሚ ሆነው መሾም አይችሉም፡፡ ደንቡም አይፈቅድም፡፡ ሌላው ደግሞ አቶ ሃይሉ መሾም አይችሉም፤ ይሄ የአልጋ ወራሽነት አሠራር አይደለም። እሳቸው ትልቅ ጂም ሠርተዋል፤ ከፈለጉ የዚያ ሃላፊ ሊያደርጓቸው ይችላሉ።

አቶ ያዕቆብ እንዲመረጡ ካልፈለጋችሁ ኢ/ር ሃይሉ ደከመኝ እያሉ ከምትመርጡ ለምን ፓርቲው በም/ፕሬዚዳንቱ እንዲመራ አላደረጋችሁም?

እኛም ያንን ነበር የጠበቅነው፤ ከደከማቸው ለሌላኛው ም/ፕሬዚዳንት መስጠት ይችላሉ፤ ያንን ባለማድረጋቸው እና አባል ላልሆነ ሰው ስልጣን በመስጠታቸው ነው ትልቁ ችግራችን፡፡ ካላወቁት መልአክ የሚያውቁት ሰይጣን ይሻላል ነው የሚለው ቃሉ፡፡ ከፓርቲው ከተለያችሁ ሁለት አመት ሆኗችኋል።

በዚህ ጊዜ ምን ሠራችሁ? የጠ/ጉባኤ ጥሪያችሁ ምን ይመስላል?

ፓርቲን የማደራጀት ስራ ነው እየሰራን የቆየነው፡፡ ፓርቲያችንን ለማንቃት እየሰራን ነው፡፡ 320 የሚሆኑ የፓርቲው ጠቅላላ ጉባኤ አባላት ፈርመው ለምርጫ ቦርድም አስገብተዋል ግን እስካሁን የተወሰነ ነገር የለም፡፡ እናንተ የምትጠይቁትን ነገር ኢንጂነር አልቀበልም ቢሉስ? የፓርቲው አባላት ይሰበሰባሉ፤ ውይይት ያደርጋሉ። ከዚያም ሁለት አመት ሙሉ የሔደበትን ለዚህ አጣሪ ጉባኤ ሪፖርት ያቀርባል፡፡ ስራ የሰራም ከሆነ የሰራውን፣ ያልሠራም ከሆነ ያልሠራበትን፤ ችግሮች ካሉ ችግሮቹን በሙሉ ያቀርብና ምርጫ ይካሄዳል፡፡ ከዚያ ከአምስት እጩዎች ውስጥ አንድ ለፕሬዚዳንትነት፣ ሌሎቹ ለምክትል ፕሬዚዳንትነት ይቀርባሉ፡፡ አቶ ሃይሉ በዚያ ጠቅላላ ጉባኤ ካልተመረጡ ውድቅ ይሆናሉ፡፡ ቦርዱም እውቅና እሚሰጠው በዚያን ጊዜ ለተመረጡት ፕሬዚዳንት እንጂ ለሌላ አይደለም፡፡ እለቃለሁ ስላሉ አይለቁም፤ አልለቅም ስላሉም አይቆዩም፡፡

አብዛኞቹ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና አመራሮች ስለፓርቲያቸውና ስለአባላት ድክመት የሚናገሩት ፓርቲያቸውን ከለቀቁ በኋላ ነው፡፡ “ለምን በፓርቲው ውስጥ እያሉ ስለችግሮቻቸው አይናገሩም?” በሚለው ዙሪያ በቅርቡ ከአንድነት ፓርቲ የለቀቁት ኢንጂነር ዘለቀ ረዲን ጋዜጠኛ ሰላም ገረመው አነጋግራለች፡፡

በአንድነት ፓርቲ ውስጥ ለምን ያህል ጊዜ ቆዩ?

አንድ አመት ከስምንት ወር ይሆነኛል፡፡ የ “ብርሃን ለአንድነትና ለዲሞክራሲ ፓርቲ” መስራች ነበርኩ፡፡ በዛን ሠአት ነው የመበታተን ፖለቲካ ለአገሪቱ ስለማይጠቅም በሚል ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ደብዳቤ ያስገባነው፡፡ በጋራ ለመስራት ማለት ነው። አንድነትና መኢአድ ጥያቄያችንን የተቀበሉን ሲሆን መኢአድ ግን “አንድነት” ከመድረክ ካልወጣ የሚል ጥያቄ አቀረበ፡፡ ይሄኔ “አንድነት”ም ብዙ ዋጋ የከፈልኩበት ነው በሚል አልወጣም አለ፡፡ እኛም በዛ ተስማምተን በጋራ ለመስራት ተቀላቀልን፡፡ በፓርቲው ውስጥ ችግር እንዳለ የገለፁት ከአንድነት ከወጡ በኋላ ነው፡፡ ከዛ በፊት ለምን አልተናገሩም? እኔ ችግሮች እንዳሉ በስብሠባ ላይ እገልፃለሁ። በፅሁፌም እናገራለሁ፡፡ እኔ ነጋዴ ነኝ፡፡ ፓርቲ ውስጥ የገባሁት ለለውጥ ነው፤ ስለ ድክመቱ ሁሌም በፅሁፍ እተቻለሁ፡፡ ለውጥ እንዲመጣ ነው ቤተሠቤንና ጊዜዬን መስዋዕት አድርጌ እየሠራሁ ያለሁት፡፡

ከመፃፍህ ባለፈ ለሚዲያ አሁን እንደተናገርከው የገለፅከው የፓርቲው ችግሮች አሉ?

ከሌሉ አሁን መግለፁ ለምን አስፈለገ? አጠቃላይ ችግሮቻችንን በቃለ ጉባኤ አስይዤ አውቃለሁ፡፡ ለምሳሌ አንዳንድ ሠዎች “አቶ አስራት ሴረኛ ናቸው” ሲሉ ሴራውን አብራራው ብዬ እከራከራለሁ፡፡ አንድ ሠው ሴረኛ ነው የምለው” ፓርቲው እንዳያድግ ወደታች የሚያደርግ እና ብቻውን ጐልቶ ለመታየት የሚፈልግ ከሆነ ነው፡፡ አንድ የፖለቲካ ፓርቲ መሪ፤ መንገድ ጠራጊ ዶዘር እንጂ እራሱን ለማሳየት የሚጥር መሆን የለበትም፡፡ ስራዎች እንዳይሠሩ ወይም ከፓርቲው መውጣት የሚፈልጉ ሠዎች እንዳይወጡ መሰናክል የምትፈጥሪ ከሆነ፣ ይሔ ነው ሴራ ማለት፡፡ ቁጭ ብለሽ ነገር ትጐነጉኛለሽ አትወጪም፤ ሊወጡ የሚፈልጉትን ደግሞ ነገር እየፈለግሽ ስስ ብልታቸውን በመምታት ብሎናቸውን ፈተሽ እንዲወድቁ ታደርጊያለሽ። ይሔንን በሚዲያ ከመናገር ይልቅ በውይይት ይፈታል ብዬ ስላሠብኩ ችዬው ኖርኩ፡፡ አሁን ግን ወቅቱ በመሆኑ ተናግሬያለሁ፡፡ እስቲ ሴራ ስለሚሉት ጉዳይ ያብራሩልኝ … ሰሜን ጐንደርን እኔ ስረከበው ለሁለት የተከፈለ ቡድን ነበር፡፡ ያንን ለማስታረቅ ከሠባት ጊዜ በላይ በአውሮፕላንና በመኪና ተጉዘናል፡፡ ግን ሊታረቁ አልቻሉም፡፡ ይሔም የሆነው ደግሞ አቶ አስራት በሠሩት ሴራ ነው፡፡ በመሀል ገብተው አንደኛውን ቡድን በማቅረብ፣ ሌላኛውን ቡድን በማራቃቸው ችግሩን መፍታት አልቻሉም፡፡ እኛ ስንገባበት ደግሞ ችግሩን ለመፍታት የሚያስፈልግ ገንዘብ እንዳይወጣ አቶ አስራት ከለከለ፡፡

\ስለዚህ ከእኔና ከሌሎች ስራ አስፈፃሚዎች ገንዘብ ተወስዶ፣ ልጆቹ ፆማቸውን እያደሩ ችግሩ በንግግር ተፈታ፡፡ አጣዬ የምትባል ቦታም ተመሳሳይ ችግር ተፈጥሮ ነበር፡፡ እኛ ግጭታችን ከፓርቲ ጋር ነው እንጂ የድንበር ግጭት አሊያም ሌላ የግል ግጭት የለብንም፡፡ በፊት ፓርቲው ለእንደዚህ አይነት ችግሮችና ለአባላት ስልጠና ገንዘብ መድቦ ይንቀሳቅስ ነበር፡፡ ልክ እኔ ስመጣ ገንዘቡን ከለከሉ፤ ምክንያቱ ደግሞ ሽባ እንድሆን ስለፈለጉ ነው፡፡ በእኛ እድሜ ያሉት ስራ እንዲሠሩ አይፈለግም፡፡ ስለዚህ ብሩን ከልክለው “ይሔው መስራት አልቻሉም” ለማለት ይፈልጋሉ፡፡ እናም “ፓርቲው ችግር ላይ ነው” ብዬ ሠዎችን አግባብቼ፣ ሠሌን ላይ እያደሩ ነው ስልጠና ወስደው ሀያ አምስት ቢሮዎች የከፈትኩት፡፡ ይሔ ሀቅ ነው፡፡ መተዳደሪያ ደንቡን በራሴ ወጪ ወደ ኦሮምኛ አስተርጉሜያለሁ፡፡ አሁን በፍኖተ ነፃነት ዌብሳይት ላይ የለቀቁት ነገር አለ፡፡ እኔ ኢህአዴግ እንደሆንኩ ገልፀዋል፡፡ ይሔን ጊዜ ይፈታዋል፡፡

ፓርቲው እንደ ኢህአዴግ እየሠራ ከሆነ ኢህአዴግ ነው ማለት ነው፡፡ ፓርቲው በርካታ የበሠሉና በእውቀት ያደጉ አባላቶችን የያዘ ነው፡፡ አመራሮቹ ግን በጣም ደካማ ናቸው፡፡ የፓርቲው አባላት በደንብ ቢሠራ ለውጥ የሚያመጡ ናቸው። ምንም ሳይሠራ ነው 25 ቢሮዎች የከፈትነው፡፡ ግን ፓርቲው እንዳያድግ የሚያደርጉ አመራሮች ናቸው። አመራሮቹ እኮ ስብሠባ ተከለከልን ብለው ዝም ብለው ይቀመጣሉ፡፡ ኢህአዴግ እስኪፈቅድ ነው የሚጠብቁት?

ከሆነስ መቼ ነው የሚፈቅድልን? እኔ በበኩሌ በየኤምባሲው እየሔዱ እንደራደር ማለታቸውን በፍፁም አልፈልገውም፡፡ የፓርቲውን ክብር ይነካል፡፡ ኢህአዴግ እራሱ እንዲደራደረን ነው መጥራት ያለብን እንጂ እኛ መሔድ የለብንም። ይሔ ከሴረኝነት የሚተናነስ አይደለም፤ ፓርቲውን ቁልቁል ይሰደዋል እንጂ አያሳድገውም፡፡ እኔ አሁንም ፓርቲውን አለቅም በአባልነት እቀጥላለሁ፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲ ማለት እኮ ሌላ መግስት ነው፡፡ ሌላ አገር ያሉት እኮ ይፈራሉ እንጂ ልመና አይገቡም፡፡ እዚህ ግን ሴራቸው ሲጋለጥ ይቆጣሉ፤ እኔ ደግሞ ውስጣቸውን ሸፍኜ የትውልድ ተወቃሽ መሆን አልፈልግም፡፡ የመልቀቂያ ደብዳቤ አስገብተህ ነው የወጣኸው? እኔ ህጋዊ መልቀቂያ አስገብቼ ነው የለቀቅሁት። እነሱ ቀንና ቁጥር የሌለው ደብዳቤ ሠጠን ይላሉ። መቼም ይሔን የሚያክል ፓርቲ የሚያስተዳድርና አስቀድሞ አገርን ይመሩ የነበሩ መሪ ደብዳቤ ሲወስዱ ቀንና ቁጥር አይተው ነው የሚሆነው፤ ግን እንደ ምክንያት ያወሩታል፡፡

አንዳንድ ሠዎች ንግግርህን ብታሳምረው ይላሉ፡፡ እኔ ግን አካፋን አካፋ፣ ዶማን ዶማ ማለት ነው የምፈልገው፡፡ ኢህአዴግ እነ አንዷለም አራጌ ስለ ነፃነት ሲናገሩ ግንቦት ሠባት አላቸው፡፡ አንድ ሠው ስለ አማራ ሲናገር፣ ነፍጠኛ፤ ስለ ኦሮሞ ሲናገር ደግሞ ኦነግ እያለ ኢህአዴግ ስም ይሠጣል፡፡ እነዚህ ደግሞ ሀሳቡን በነፃነት የተናገረንና ችግራቸውን የገለፀ ሠው ኢህአዴግ ነው ይላሉ፡፡ እንደውም ዶ/ር ነጋሶ ናቸው ኢህአዴግነታቸውን ይዘው የመጡት። ምክንያቱም የመናገር ነፃነታችንን እየነፈጉን ነው ያሉት፡፡ ለምሳሌ ፍኖተ ነፃነት ስለ እኔ የተሳሳተ ነገር በዌብሳይቷ ይዛ ወጥታለች፡፡ ታዲያ ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ በምን ለይቼ አያታለሁ፡፡ አዲስ ዘመን የአቶ ሀይለማርያምን ሃሳብ ይዞ ከወጣ በኋላ፣ የእኛን ግን አያወጣም፡፡ ፍኖተ ነፃነትም እያደረገ ያለው እንደዛ ነው፡፡ ችግሮችን ከፓርቲ ወጥቶ ከማውራት ለመፍታት መሞከር አሊያም ከወጡ አለመናገሩ አይሻልም? ለትውልድ እዳ ማስቀመጥ አልፈልግም። ለህዝብም ግልፅ ነገር ተናግሬ ነው መልቀቅ የምፈልገው፡፡ ከእኔ ብዙ ነገሮች የሚጠብቁ ሠዎች ይኖራሉ፡፡ ስለዚህ ችግሮቹን ለመፍታት ጥረት አደርጋለሁ፡፡ አልሳካም ካለኝ ደግሞ ችግሩን ለሚዲያ እናገራለሁ፡፡ ለምሳሌ ዶ/ር ነጋሶን እንውሠድ ዶ/ር ናቸው፡፡

ፒኤች ዲ የሚኮነው ከመሬት ተነስቶ አይደለም፤ የፊሎሶፊ ዶክተር ናቸው፡፡ አንድ እንደ እኔ በእድሜና በትምህርት የሚያንሳቸውን አርቅቆ ሠው ማድረግ መቻል አለባቸው፤ እሳቸዉ ግን እንዲማር ሳይሆን እንዲማረር ነው የሚያደርጉት። አንድ ሠው አንድ መፅሔት ላይ ስለ እኔ ፅፏል፡፡ በትልቅነታቸው ቢያከብራቸው ብሏል፤ ነገር ግን ፖለቲካ ላይ ሽማግሌ ብሎ ነገር የለም፤ እንደዚህ ያለው ነገር የሚሰራው ሠፈርና እድር ውስጥ ብቻ ነው፡፡ አብዛኞቻችን እኮ አገራችንን አንወድም። እዚህ አርግዘን አሜሪካን ወልደን ለመምጣት የምንፈልግ ነን፡፡ ሌሎቹ እኮ እዚህ አርግዘው ለመውለድ አገራቸው ነው የሚሔዱት፡፡ ለፓርቲው አድርጌለታለሁ የሚሉት ነገር ምንድነው? በገንዘብም በጉልበትም ብዙ ነገር አድርጌለታለሁ። ይሔንን መጥቀስ አያስፈልግም።

ዶ/ር ነጋሶ ለጀርመን ሬድዮ ሲናገሩ ገንዘቡን እንደፈለገ ሊረጨው ስለፈለገ ነው ብለዋል፡፡ እኔ ገንዘቡን ብረጨውና አባላቱ ከመጡ፣ እሳቸው የሚፈልጉት ይሔንን አይደለም እንዴ? ግን ያልሆነ ያልተደረገ ነገር ሲወራ ያሳዝናል፡፡ ፓርቲውን ቢመራው ብለው የሚያስቡት ማንን ነው? አቶ ተክሌ የፋይናንስ ሀላፊ ናቸው፡፡ እሳቸው ቢመሩት ከፍተኛ ለውጥ እንደሚመጣና የተሻለ ስራ እንደሚሠሩ አምናለሁ፡፡ ከዚህ በኋላስ ምን ለማድረግ አስበዋል? ፓርቲዬን አልተውም፤ በአባልነት እቀጥልላለሁ። እንደዚህ አይነት አመራሮች ፓርቲውን እንዳያሽመደምዱት የበኩሌን እጥራለሁ፡፡

ለአንድ መንግሥት ህልውና ከሚያስፈልጉት ጉዳዮች ቀዳሚው የሚመራውን ህዝብ ሰላምና ፀጥታ ማስከበር ነው፡፡ ደረቱን ነፍቶ ግብር የማስከፈል መብት እንዳለው ሁሉ የህዝብን ሰላምና ፀጥታ የማስከበር ግዴታውን ካልተወጣ መንግስትነቱ ለአደጋ ተጋልጧል ማለት ነው፡፡ ኢህዴግ በጉልበቱም ቢሆን በትረ መንግስት እንደጨበጠ ሰሞን ሌባንና ዘራፊን ተግቶ በመከላከሉ በህዝቡ ዘንድ መልካም ተቀባይነት ነበረው፡፡ አባላቱም ከሞላ ጐደል ጨዋዎችና ቁጥቦች ነበሩ፡፡

የመጡበት ማህበረሰብ (ገጠሬው) ጨዋና የሞራል ባለቤት ስለሆነ ስግብግቦችና አታላዮች አልነበሩም፡፡ የስልጣን ክፍፍል ሲጀመር፤ አንዳንዶች በቅጽበት ባለ ዘመናዊ መኪኖችና የሰማይ ጠቀስ ፎቆች ባለቤት ሲሆኑ፤ ትላንት የኔ ቢጤ የነበረው በቅጽበት “አንቱ…” የተሰኘ ባለፀጋ ሆኖ ሲመለከት ጨዋው ሁሉ ኢትዮጵያዊ ይሉኝታና ዕምነቱን እንደ ጨርቅ አውልቆ መጣል ጀመረ፡፡ በቅጽበት ለመበልፀግ ሲልም በአቋራጭ የመክበሪያ ሩጫውን ተያያዘው፡፡ በአቋራጭ ለመክበር የቆረጠ ሰው ከበዛ ደግሞ ህግና ህጋዊነት አደጋ ላይ ይወድቃሉ፤ ወድቀዋልም፡፡

ትላንት ከትላንት በስቲያ በኬንያና ናይጀሪያ እንሰማው የነበረው ጉቦኝነት፣ አገራችን ውስጥ ያለሃይ ባይ ሰተት ብሎ ገባና ቁምስቅላችንን ያሳየን ጀመር፡፡ ምንም አይነት ቀላል ጉዳይ ቢሆን ሊከናወን የሚችለው በመደለያ ነው፡፡ ይህ አደገኛ ጉዞም ህዝቡን ቁምስቅሉን እያሳየው መጣ፡፡ “ኑሮ ጣራ ደረሰ፤ ኧረ የመንግስት ያለህ!” ሲባል “የኑሮ ውድነቱን ያመጣው ዕድገቱ ነው” የሚል የዋህ ወይም የጅል መልስ ይሰጣል፡፡ እርግጥ ነው ባለስልጣኖቻችን ከህዝብ በሚሰበሰብ ሃብት ባለሁለትና ከዚያም በላይ ዘመናዊ መኪኖች እንዲገዙላቸው ወይም እንዲመደቡላቸው ልዩ ዕድል ተሰጥቷቸዋል፡፡ የአብዛኞቹ ባለስልጣናት ልጆች የሚማሩት ከወር ደሞዛቸው በላይ በወር በሚያስከፍሉ ዓለም አቀፍ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ነው፡፡

ግን ገንዘቡ ከየት እንደሚመጣ እነሱና እግዜር ብቻ ናቸው የሚያውቁት፡፡ የቤት መስሪያ ቦታ ብዙውን ጊዜ 500 ሜ.ካሬ ቦታ ይሰጠቸውና (የመስሪያ ገንዘብ እንደሚመቻችላቸውም ይነገራል) የተንጣለለ ቤት ሰርተው፣ በወር 50 እና 30ሺህ ብር እያከራዩ የሚኖሩት ከመንግስት በሚሰጣቸው ምርጥ ቪላ ውስጥ ነው፡፡ ለሰፊውና በኪራይ እሳት ለሚጠበሰው ነዋሪ ግን ስንት ዓመት ደጅ ጠንቶ የሚሰጠው (ከ97 ወዲህ እሱም ቀርቷል) 72 እና ከበዛም 94 ሜትር ካሬ ነው፡፡ የቤት ፍላጐት ባለመሟላቱም ህዝቡ ከጅብ ጋር እየታገለ ሌሊት የወፍ ጐ ጆ የምትመስል ደሳሳ መጠለያ ሲያውገረግር ያድራል፡፡ ከመንግስት ጋር በአንድ ወይም በሌላ ንክኪ ያለው ደግሞ የአዲስ አበባንና የፊንፊኔ ዙሪያ ገባ መሬት እንደ ልቡ ይቸበችባል፡፡ (ራሱ መንግስት ያመነው ነው) በሰፊው መሬት የያዘውንና እንደ ራሱ ሃብት እንደ ልቡ የሚጨፍርበትን ማንም አይናገረውም፡፡ ሲፈራ ሲቸር የእንጨት ጐጆ ቀልሶ በሁለት ስጋቶች ተወጥሮ የሚኖረውን ምስኪን የኔ ቢጤ ግን ጐጆው በላዩ ላይ በግሬደር ስትፈርስበት ደጋግመን ታዝበናል፡፡

ሁለት ስጋቶች ያልሁት አንደኛው መብራትና ሌሎች የመሠረተ ልማት አገልግሎቶች በሌሉበት ቤተሰቡን በአውሬ እንዳይነጠቅ፤ ጥቂትም ብትሆን ያለችው ጥሪቱ በወሮበሎች እንዳትዘረፍ ቀን የትም ሲኳትን ውሎ ሌሊትም በስጋት ሲባዝን ማደሩ ሲሆን፤ ሁለተኛው ስጋቱ ደግሞ ያችኑ የጭራሮ ቤቱን “መንግስት ድንገት መጥቶ ቢያፈርስብኝ የት እገባ ይሆን?” ከሚል ጭንቀት የሚመነጭ ነው፡፡ በመሠረቱ ህገወጥነት የሚበራከተው ከቅንጦት አይደለም፡፡ መንግስት መስራት የሚገባውን በጊዜ ባለማድረጉ ፤ ህዝባዊ ጥያቄዎች በወቅቱና በአግባቡ ተግባራዊ ምላሽ ሳይሰጥባቸው ሲቀር፤ በአንፃሩ ጥቂት ህገወጦች በቆረጣ ሲበለጽጉ ሲያይ ጨዋ የነበረው ሁሉ ወደ ህገወጥነት ይገባል - መንግስት በፈጠረው ጣጣ፡፡ የቀበሌም ሆኑ የክፍለ ከተማ ባለስልጣናት የሚኖሩት በህዝቡ መሃል ነው፡፡ “ህገወጥ” የሚባለው የመሬት ወረራ ሲካሄድም ያያሉ፤ ግን ትንፍሽ አይሉም፡፡ ይህን የሚያደርጉት በሁለት ምክንያት ነው ብሎ መገመት ይቻላል፡፡ አንደኛው ቤቱ ከተሰራ በኋላ “ላፈርስብህ ነውና ይህን ያህል ገንዘብ አምጣ” ለማለትና ለህገወጥ ብልጽግና ነዋሪውን ለማመቻቸት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በስልጣን ላይ ሳሉ እነሱም የጨዋታው ተዋናይ በመሆን በቤተሰባቸው ወይም በዘመድ አዝማድ ስም የሃገሪቱን መሬት ተቀራምተው ዘወር ለማለት ነው፡፡ ይህ እውነት መሆኑን የምናውቀው ሚያዝያ 28 ቀን 2005 ዓ.ም ማታ “የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በህገ ወጥ መንገድ ስለተያዙ ቦታዎች ሊያወጣው ነው” ስለተባለው መመሪያ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የተነገረውን ዜና በወጉ ስንመዝነው ነው፡፡ በመጀመሪያ “ህጋዊ የሚሆኑት ከ1988 ዓ.ም በፊት ይዘው የነበሩና ይዞታቸው ለመሆኑ የመሬት መጠቀሚያ ግብር የከፈሉበት ደረሰኝ ያላቸው ብቻ ናቸው” ሲባል ነበር፤ ቀጥሎ ደግሞ “እስከ 1994 ዓ.ም ባሉት ጊዜያት ቤት የሰሩ” ተባለ፤ ለሶስተኛ ጊዜም “እስከ 1997 ባሉት ጊዜያት የተያዙ ይዞታዎች ብቻ ህጋዊ ይሆናሉ” ተብሎ ሽርጉድ በዝቶ ነበር፡፡

በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ የሰማነው ግን “እስከ ህዳር 2004 ዓ.ም የተሰሩ ህገወጥ ግንባታዎች ሁሉ ህጋዊ እውቅና ይሰጣቸዋል” የሚል ነው፡፡ የጽሑፌ ዓላማ “በህገወጥ መንገድ ቤት ለሰሩ ዜጐች ለምን ህጋዊ ዕውቅና ተሰጣቸው” የሚል ተራ ምቀኝነትና ክፋት አይደለም፡፡ ይልቁንም መንግስት ዜጐቹን መፈናፈኛ እያሳጣ ለችግርና ለህገወጥነት እንዴት እንደሚገፋፋቸው፤ ህገወጥነትን ለመቆጣጠርም አቅም እያጣ መምጣቱን ማሳየት ነው፡፡ ነዋሪው በየቀኑ እንደ ሮማን ፍሬ ከተሞችን አጨናንቆ ሊያነዳቸው ደርሷል፡፡ በገጠር ያሉ ወጣቶች በአዋጅ የተገደዱ እስኪመስሉ ድረስ በየቀኑ ወደ ከተሞች፤ በተለይ ወደ አዲስ አበባ ይጐርፋሉ፡፡ ከተማ ውስጥ በቂ ሥራ የለም፡፡ ዲግሪ ይዞ የሻይና የታክሲ መሳፈሪያ እያጣ ሳንቲም የሚለምን ወጣት እያየን ነው፡፡ ነዋሪ በበዛ ቁጥር የመኖሪያ ቤት ኪራይ ሰማይ ይነካል፡፡ ኪራይ ሲጨምር ዜጐች መፈጠራቸውን እስኪጠሉ ድረስ በኑሮአቸው ይንገሸገሻሉ፡፡ የአከራዮች ጭካኔ ወደር የለውም፡፡ መንግስት የጋራ ህንፃዎችን ለመገንባት ተፍተፍ ማለቱ የሚካድ ባይሆንም ከነዋሪው ፍላጐት ጋር የሚመጣጠን ባለመሆኑ የጠብታ ያህል እንኳ ችግሩን መፍታት አልቻለም፡፡ በዚያ ላይ ብዙ ገንዘብ ወጥቶባቸው የተገዙና የታደሱ ቤቶች አመት ሳያገለግሉ ሊፈነገሉ መድረሳቸውን እያየን እየሰማንም ነው፡፡ (ጀሞ ሳይት ላይ የተፈጠረውን ልብ ይሏል) ይህ የሚያመለክተው የ “እንካ በእንካ” ሥራ ውጤት መሆኑንና የጥራት ጉዳይ ትኩረት እንደተነፈገው ነው፡፡

ባለስልጣናቱ ለተሰጣቸው ኃላፊነት ሳይሆን ለመሞዳሞድ ቅድሚያ የሰጡ ይመስላሉ፡፡ ይህ ካልሆነ ተቆጣጣሪ መሃንዲሱ የት ነበር? በየጊዜው “ሳይቶችን ሲጎበኙ” የምናያቸው ባለስልጣናትስ ምኑን ነው ሲጎበኙ የከረሙት? ነዋሪው ተበድሮም ሆነ በአቅሙ ቤት ለመስራት ቦታ እንዲሰጠው የባለስልጣናትን ደጅ መጥናት ሰልችቶታል፡፡ በህጋዊ መንገድ ጠይቆ ህጋዊ መልስ ሲያጣ ወደ ህገወጥነት ያመራል፡፡ አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ሲጠቀም የሚስተዋለው ህግን አክብሮ መንግስትን አምኖ የተቀመጠው ሳይሆን ህግን መረጋገጫቸው ያደረጉ ባለስልጣናትና ህገወጥ ግለሰቦች ናቸው፡፡ በመሠረቱ ኢትዮጵያ የሁላችን ሃብት ናት፤ መከራዋ መከራችን፤ ደስታዋ (አይተንባት ባናውቅም) ደስታችን ነው፡፡ አብዛኞቹ የመንግስት ባለስልጣናትና ካድሬዎች የሚያስቡትና የሚተገብሩት ግን በግልባጩ ነው፡፡ አገሪቱን እንደ ግል ሃብታቸው፤ ህዝቡንም እንደ መጫወቻ አሻንጉሊታቸው የመመልከት አባዜ ተጠናውቷቸዋል፡፡ ለዚህም ነው ንግግር ባደረጉ ቁጥር “ህዝባችን፣ አርሶ አደራችን! …” እያሉ የሚመጻደቁት፡፡ በመሠረቱ የእነሱ የግል ሃብት የሆነ ህዝብ የለም፤ ኢትዮጵያዊ ህዝብ ግን አለ፡፡ የእነሱ የሚባል አርሶ አደርም የለም፤ ፋትሮና መከራ አይቶ የሚኖር አርሶ አደር ግን በሽ ነው፡፡ እንደሚመስለኝ ይህ በሽታ የተጠናወታቸው ከአፄው ስርዓት ነው፡፡ ንጉሡ ሲናገሩ “የሚወደንና የምንወደው ህዝባችን …” ማለት ያዘወትሩ ነበር፡፡ ግን ሁለቱም የምር ባላንጣዎች እንደነበሩ በ1966 ዓ.ም በተካሄደው አብዮት ተመልክተናል፡፡ ኢህአዴግ በርካታ ህጐችን በማውጣት የሚቀድመው የለም፡፡ ግን ቀድሞ ህግጋቱን የሚጥስ ራሱ ነው፡፡ “እሞትለታለሁ” እያለ የሚምል የሚገዘትበት ህገ መንግስቱ፤ ማንኛውም ዜጋ በሃገሪቱ ውስጥ ተዘዋውሮ የመስራትና ሃብት የማፍራት መብት እንዳለው ይደነግጋል፡፡

ግን በመጣበት መንደር እየተለየ መከራ የሚያየውና በገዛ አገሩ ላይ ስደተኛ የሆነው ህዝብ እጅግ በርካታ ነው፡፡ ለምሳሌም ወለጋ፣ ጉራፈርዳና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ላይ የተፈፀመውን ማስታወስ በቂ ነው፡፡ በ1997 ዓ.ም ላይ በየክልሉ በታሪክ ታይቶ የማይታወቅ ግብር ተጣለ፡፡ በዚህም የንግዱ ማህበረሰብ አባላትና ቤተሰባቸው እጅግ አዘነ፤ አቤት ቢልም የሚሰማው አጣ፡፡ ባለታክሲዎች ላይም ተመሳሳይ ድርጊት ተፈጸመ፡፡ ቅሬታ የሚቀበል ባለስልጣንና የቅሬታ ማስተናገጃ ስርዓትም አልነበረም፡፡ “ማብቃት” በሚል ማደናገሪያ ቃል በርካታ የአማራ ክልል ሰራተኞች የስራ ዋስትናቸውን አጥተው ለከፍተኛ ችግር ተዳረጉ፡፡ ለዚህም ይግባኝ የሚባልበት አካል አልነበረም፡፡ በአጠቃላይ “ይህ መንግስት መንግስቴ ስለሆነ ህግና ስርዓቱን አክብሬ መጓዝ አለብኝ” የሚለው ቁጥር እጅግ እየቀነሰ መጥቶ “ምን አለ ከዚህ መንግስት የሚገላግለኝ ተዓምር ቢፈጠር” ባዮች በረከቱ፡፡ በመጨረሻም ምርጫ 97 መጣና ኢህአዴግ ልኩን የሚያውቅበት አጋጣሚ ተፈጠረ፡፡ ከዚያ በኋላ የሆነውን የምናውቀው ነው፡፡ ሌላም ህግ የሚጣስበትን መንገድ ልጠቁም፡፡ የመናገር፣ የመደራጀት፣ የመሰብሰብና የጽሁፍ ነጻነት በህገ መንግስቱ ላይ ሰፍሯል፡፡

በተግባር ግን እጅግ ብዙ ይቀረዋል፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች/ተቃዋሚ ናቸው ብለን እንቀበልና ስብሰባ ሲጠሩ በሰበብ አስባቡ እንዲደናቀፍባቸው ይደረጋል፡፡ በመሆኑም በግልፅ መሰብሰብ ካልቻሉ በህቡዕ ለመንቀሳቀስ ሊገደዱ ይችላሉ፡፡ ጋዜጠኞች ማስረጃ እስካላቸው ድረስ በፈለጉት ርዕስ ላይ መጻፍ ካልቻሉ ስደትን ይመርጣሉ፡፡ ወይም ህሊናቸው ዓመጽ ያረግዛል፡፡ ሙስና ከምንም ጊዜ በላይ እየከፋ መጥቷል፡፡ አሁን የቀረው አንድ ነገር ብቻ ነው፡፡ ወደ ፓርላማ ወስዶ “ሙስናን ህጋዊ አድርጉልን፣ በሙስና ልናገኘው የሚገባንን ሃብት መጠንም በአዋጅ ወስኑልን” ማለት፡፡ ለዚህ ሁሉ ጣጣ መንስኤው የባለስልጣናት ፍርደ ገምድልነት ነው፡፡ ከላይ እንደ ጠቀስሁት በመሬት ወረራ ላይ የተሰማሩትን ሰዎች ወደ ህገ ወጥነት የገፋፋቸው ራሱ መንግስት ነው፡፡ የመሬት ጥያቄ ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ቢመለስ ነዋሪው “ነገ ይፈርስብኛል” በሚል ስጋት ስጋው እያለቀ ወደ ህገወጥነት አያመራም ነበር፡፡ ለስንት ጊዜ ደጅ ጠንቶ፣ በማህበር ተደራጅቶና ስምንት ሺህ ብር በዝግ ሂሳብ አስቀምጦ ያገኘው ቦታ መጠን እንኳን ለሰው ለአህያ ማሰሪያ የሚበቃ አይደለም፡፡ እሱም ከ1977 በኋላ ከአነካቴው ቆሟል፡፡

ታዲያ ዜግነት ትርጉሙ ከምን ላይ ነው? ጐጆውን የሚቀልስበት የበሬ ግንባር የምታህል መሬት ካላገኘ፤ በኑሮው ላይ ለውጥ ማየት ካልቻለ፤ የትምህርት ቤት፣ የትራንስፖርት፣ የቤት ኪራይና የዳቦ መግዣ አጥቶ የተወለደበትን የሚረግም ከሆነ፤ በአንፃሩ የአገሪቱ ሃብት እጅግ ጥቂት በሆኑ ግለሰቦች እጅ ከተግበሰበሰ፣ ነገ ምን ሊፈጠር እንደሚችል መገመት ነቢይ መሆንን የሚጠይቅ አይደለም፡፡ ስለሆነም መንግስት ምክንያታዊ የሆነ ህግ ማውጣትና ሚዛናዊ የሆነ አተገባበር ልምድ ሊኖረው ይገባል፡፡ አለዚያ ትላንት ያወጣውን ህግ ራሱ እየሻረ፣ ህዝቡን ግራ የሚያጋባ ከሆነ “መንግስት ባይኖርስ?” ወደሚል ጥላቻ ያመራል፡፡ መንግስት ህግን አክብሮ የማስከበር አቅሙን ካላዳበረ፤ የቦታ ጥያቄን በአግባቡና በፍጥነት ካልመለሰ የነዋሪው ችግር በራሱ ላይ የሚመጣ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም መንግስት በህገ ወጥ መንገድ ለተፈፀመ ድርጊት ሁሉ ህጋዊ እውቅና የሚሰጥ ከሆነ መቼም ቢሆን ህጋዊነት ሊኖር አይችልም፡፡ ስለዚህም መንግስት የህዝብ ሞግዚትነቱን አይዘንጋ፤ ህግን ያክብር፤ ህግን በአግባቡ ያስከብር፤ የግለሰቦቹ ሞግዚት ሳይሆን የህዝብ ወኪል ይሁን፡፡