በፋሲል ኃይሉ የተገጠሙ ሃምሳ ሦስት አጫጫርና መካከለኛ ግጥሞች የተካተቱበት “ፎርፌ” የግጥም መጽሐፍ ከማተሚያ ቤት ወጥቶ ለንባብ በቃ፡፡ ገጣሚው በምስጋና ገጹ “ያነሳሁአቸው ሀሳቦች የእኔ ብቻ ሳይሆኑ የጓደኞቼም ናቸው” ያለበት የግጥም መጽሐፍ 74 ገፆች ያሉት ሲሆን የታተመውም በፋርኢስት ትሬዲንግ ኃላ.የተ.የግል ማህበር ነው፡፡ “ፎርፌ” በ22 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

በኩራት ፒክቸርስ ኃ/የተ/የግ/ማህበር በዳይሬክተር ይድነቃቸው ሹመቴ ተጽፎ የተዘጋጀ “ኒሻን” የተሰኘ ፊልም ማቅረቡን አስታወቀ፡፡ ተሠርቶ ለማጠናቀቅ አንድ ዓመት የፈጀው የ104 ደቂቃ ፊልም የሚመረቀው እሁድ ግንቦት 4 በአዲስ አበባ በሚገኙ የግል ሲኒማ ቤቶች ነው፡፡ በልብ ሰቀላ ድራማ ፊልሙ ላይ ብርትኳን በፍቃዱ፣ ፈለቀ አበበ፣ ቴዎድሮስ ስፍራዬ፣ አለባቸው መኮንን፣ አላዛር ሳሙኤል፣ ተዘራ ለማ እና ሌሎችም ተውነዋል፡፡ ይድነቃቸው ሹመቴ ካሁን ቀደም “ስርየት” የተሰኘ ፊልም ዳይሬክት ማድረጉ ይታወቃል፡፡

Saturday, 04 May 2013 11:37

ኢትዮ-ቴሌኮምና ችግሮቹ

“የስልክ ጥራት ችግር ከእድገቱ ጋር የመጣ ነው”

የቴሌኮምኒኬሽን አገልግሎት የጥራት መጓደል ቀድሞም የነበረው ጉዳይ ቢሆንም ከቅርብ ጊዜያት በተለይም በሣምንታት እድሜ ከሚቆጠር ጊዜ ወዲህ ዘርፈ ብዙ ችግሮች እየተስተዋሉበት ነው። በሞባይል እየተነጋገሩ አገልግሎት በድንገት ተቋርጦ አየር ላይ መቅረት፣ የድምፅ በጥራት አለመሠማት፣ በአንድ አካባቢ ካለ ወዳጅ ጋር እንኳ መገናኘት አዳጋች እየሆነ ነው፡፡ በተመሣሣይ ዘመኑ የፈቀደውን በይነ መረብ (ኢንተርኔት) አገልግሎት ለመጠቀም ብንሞክርም ከመንቀራፈፉም በላይ እንደ ሞባይል ንግግሩ እሡም የሚቆራረጥበት ጊዜ ይበረክታል፡፡ የመደበኛ (መስመር) ስልክም ቢሆን ሲበላሽ ለማስጠገን የገነት መግቢያ ያህል መትጋትን የሚጠይቅ ከሆነ ሠነባብቷል፡፡ ታዲያ የጉዳዩ ዋነኛ ባለቤት የሆነው ኢትዮ ቴሌኮም እነዚህ መሠረታዊ የጥራት ችግሮች እንዴት አጋጠሙት፣ በቀጣይስ በምን አግባብ ሊፈታቸዉ አሠበ ስንል ጠይቀናል፡፡ በኢትዮ - ቴሌኮም የኮርፖሬት ኮሚኒኬሽን ሃላፊው አቶ አብዱራሂም አህመድም ለጥያቄያችን ምላሽ ለመስጠት በርካታ ቀናት ያህል በተለዋዋጭ ቀጠሮዎች ቢያቆዩንም ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር በነበራቸው ቆይታ በተነሡት ርዕሠ ጉዳዮች ዙሪያ ተነጋግረዋል፡፡

የተንቀሣቃሽ ስልክ አገልግሎት የኔትወርክ መቆራረጥ፣ የድምፅ ጥራት መቀነስ የመሣሠሉት ችግሮች በስፋት እየተስተዋሉ ነው፡፡ ኢትዮ ቴሌኮም እነዚህን ለማስተካከል ምን እርምጃ እየወሠደ ነው? የተንቀሣቃሽ ስልክ ኔትወርክ እና መቆራረጥ ችግሮች በዋናነት በሁለት ልንከፍላቸው እንችላለን። የመጀመሪያው አዲስ አበባ ላይ የሚታዩት ናቸው፡፡ አዲስ አበባ ደግሞ ተለይተው የሚታወቁ ቦታዎች አሉ፡፡ የኖክያ አካባቢ የሚባል አለ፣ ከአስኮ ጀምሮ በኮልፌ ቀራኒዮ በአስራ ስምንት ማዞሪያ፣ በሉካንዳ፣ አለምገና፣ አየር ጤና፣ መካኒሣ፣ ካራቆሬ፣ ቄራ እና እስከ ሃና ማርያም የሚደርስ፡፡ ይሄ ከ10 አመት በፊት የተተከለ ነው፡፡ እዚህ አካባቢ ያለው ተጠቃሚ አገልግሎቱን በአግባቡ እያገኘ አይደለም። ይሄ የሚታወቅ ነው፡፡ መፍትሄው ሁለት ነው። አንደኛ ጊዜያዊ መፍትሄ አለ፤ ሁለተኛው ቋሚ/ዘላቂ የሚባለው ነው፡፡ ጊዜያዊ መፍትሄ ስንል በዚህ በጠቀስኳቸው ቦታዎች ያለውን ኔትወርክ የማሣደግ ስራ ነው፡፡ ዘላቂው ስራ ደግሞ ይሄንን ሙሉ ለሙሉ በአዲስ የመቀየሩ ስራ ነው፡፡ አሁን ጊዜያዊ መፍትሄው እየተሠራ እያለ ሙሉ በሙሉ የመቀየሩ ስራ ግን በጥቂት ወራት ውስጥ ተሠርቶ ይጠናቀቃል ማለት ነው፡፡

በዋነኛነት አዲስ አበባ በተቋሙም እንደሚታወቀው የአገልግሎት ጥራት ችግር አለ፡፡ በአካባቢው ያለው ከአምስት አመት በፊት የተዘረጋ ኔትወርክ ነው፡፡ ለምሣሌ እንደ ጀሞ፣ ለቡ ያሉትን ብንወስድ መሠረተ ልማት ከመዘርጋቱ በፊት በዚያ አካባቢ የነበረው ነዋሪ በጣም ትንሽ ነው፡፡ አሁን ግን ጀሞን ብቻ ብንወስድ ከ40ሺህ በላይ ነዋሪ ያለበት ነው፡፡ እና ይሄንን በየጊዜው የማሣደግ ስራ እንዳለ ሆኖ የመቀየርና የማሣደግ ስራ ይሠራል፡፡ እዚህ አካባቢ ተጠቃሚው አገልግሎቱን በተገቢው መልኩ እያገኘ አይደለም፡፡ ሁለተኛ አዲስ አበባን አጠቃላይ ስንወስድ ከኔትወርክ ጥራቱ ችግር ጋር የምናነሣው የህንፃዎችን ማደግ ነው፡፡ ህንፃዎች ሲያድጉ የቴሌኮም አንቴናዎች በአንፃሩ የተተከሉት መሬት ላይ ነው፡፡ አሁን ኔትወርኩን ለማሣደግ አንቴናዎች ህንፃዎች ላይ መተከል አለባቸው፡፡ ግን ይህን ለማድረግ እስከ አሁን ፈቃደኛ የሆነ ባለ ህንፃ የለም፡፡ ነገር ግን በህጉ የተቀመጠ አለ፡፡

የትም ቦታ በአግባቡ የቴሌኮም መሠረተ ልማት የመዘርጋት ግዴታ አለ። ይህም ሲባል ተገቢውን ክፍያ በመክፈል ነው፤ ሌላው ተደጋጋሚ የኤሌክትሪክ ሃይል መቆራረጥ እያጋጠመን ነው። እያንዳንዱ አንቴና በኤሌክትሪክ ሃይል ነው የሚሠራው፡፡ የኤሌክትሪክ ሃይል ሲቋረጥ ችግሩ ይፈጠራል፡፡ ሌላው የተጠቃሚው ቁጥር መጨመር ነው፡፡ በ2002 ያለው 6.7 ሚሊዮን ነበር አሁን ያለው 22 ሚሊዮን ተጠቃሚ ነው። በአጠቃላይ ጥራቱ ላይ የሚስተዋሉት ችግሮች እነዚህ ሲሆኑ ከእድገቱ ጋር የመጡ ናቸው፡፡ መቼ ነው ታዲያ የሚስተካከለው? በጥቂት ወራት ውስጥ፡፡ አሁን ይሄንን መሠረተ ልማት ለመቀየር የሚያስችል ስራ እየሠራን ነው፡፡ ይሄ ስራ በቅርቡ ይጠናቀቃል፡፡ የቅድሚያ ቅድሚያ ተሠጥቶት የሚሠራው ዝርጋታውን የማቀላጠፍ ስራ ነው፡፡ የሃይል መቆራረጡን በተመለከተ ለእያንዳንዱ አንቴና ብቻ ሣይሆን አቀባባይ ለምንላቸው ጄኔሬተር የማቅረብ ስራ እየሠራን ነው፡፡

ከህንፃዎች ጋር ያለውንም ከባለ ህንፃዎች ጋር በመነጋገር ወደ ስራው በመግባት ነው ችግሩ የሚፈታው፡፡ የኢንተርኔቱ መቆራረጥስ ከምን ጋር ነው የሚያያዘው? የኢንተርኔቱን መቆራረጥ በሁለት መልኩ ልናየው እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው የፋይበር ኦፕቲክ ገመድ መቆረጥ ጋር እናያይዘዋለን፡፡ የፋይበር ኦፕቲክስ ፋይበር አሁን በሃገራችን ከ12 ሺህ ኪሎ ሜትር በላይ ተዘርግቷል፡፡ በ45 አቅጣጫዎች ማለት ነው፡፡ ይሄ ዋነኛ አላማው የሃገር ውስጡን ግንኙነት ማቀላጠፍ ነው፡፡ ለአለማቀፍ ግንኙነት የምንጠቀምባቸው ደግሞ ሶስት አቅጣጫዎች አሉ፡፡ ከአዲስ አበባ - መተማ አድርጐ ፓርት ሱዳን የሚሄደው፣ ሁለተኛው ከአዲስ አበባ ጅቡቲ የሚሄደው፣ ሶስተኛው ከአዲስ አበባ በሃዋሣ አድርጐ ሞያሌ ሞንባሣ የሚደርሠው ነው፡፡

ይህ ፋይበር ኦፕቲክ እንግዲህ እየሠጠ ያለው አገልግሎት ሁለት ነው፡፡ አንደኛ የሃገር ውስጡን ትራፊክ ይሸከማል። ሁለተኛ አለማቀፍ ግንኙታችንንም ያከናውናል። ወደ ኢንተርኔት ስንመጣ ለኢንተርኔት ግንኙነት ከሣተላይት በተጨማሪ በእነዚህ ሶስቱ መስመሮች ነው ግንኙነታችን፡፡ እነዚህ ሶስቱም ወደ ባህር ሄደው በባህር ጠለቅ ኬብል አድርገው ጄዳ፣ ከዚያ ለንደን ደርሠው ነው የአለማቀፍ ግንኙነታችንን የሚያሳልጡ፡፡ እንግዲህ ፋይበር ኦፕቲክ ኬብል ተቆረጠ ማለት በድሮው ከሆነ አገልግሎት ይቋረጣል ማለት ነው፡፡ ለምሣሌ ከዚህ መተማ ያለው ደባርቅ ላይ ቢቋረጥ፣ አንደኛ የባህር ዳር አካባቢ ግንኙነት ይቋረጣል፡፡ ከዛ አልፎ በፖርት ሱዳን አድርጐ የሚሄደው ግንኙነታችንም ይቋረጣል፡፡ አሁን ግን እዚያ ደረጃ አይደለንም፤ በማይክሮዌቭ እንገናኛለን።

ሁለተኛ በቀለበት መልኩ የተዘረጋ ስለሆነ ደባርቅ ላይ ቢቋረጥ ባህር ዳርን በመቀሌ ወይም በደሴ አድርገን እናገኘዋለን፡፡ በዚህ መፍትሄ አገልግሎቱ አይቋረጥም ግን ጭነቱ በትክክል ወደሚሠራው ይመጣል፡፡ በዚህ ጊዜ የኢንተርኔት ግንኙነት በጣም ይጓተታል ማለት ነው፡፡ አንዱና ትልቁ ችግር እሡ ነው፡፡ ይህ በአለማቀፍ ደረጃም ያጋጥማል፡፡ አሁን እኛ በሶስት ባህር ጠለቅ ኬብል በምንገናኝበት ላይ በቅርቡ ያጋጠመ አለ፡፡ በሜዲትራኒያን አካባቢ ተቆርጦ ከሰባት ቀን በላይ አገልግሎት የመጨናነቅ ሁኔታ ነበር፡፡ ከ177 ሠአታት በላይ ተቋርጧል፡፡ ይሄ እንግዲህ ከእኛ አቅም ውጪ የሆነ ነው ማለት ነው። ይህ በሚቋረጥበት ጊዜ ተጠቃሚው በአግባቡ አገልግሎቱን አያገኝም ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው በከተማ ውስጥ ተደጋጋሚ መብራት በሚቋረጥበት ጊዜ ማስተላለፊያ ሣጥኖች አሉ፤ ድሮ ኬብል ካቢኔት የምንላቸው ማለት ነው፡፡ ከ45 አመት በፊት ተተክለው የነበሩና በመዳብ የሚሠሩ ናቸው፡፡

እነዚያ አሁን ከአራት አመት በፊት ነው የተቀየሩት። እነዚያ የራሣቸው የአቅም ውስንነት ነበራቸው፡፡ አቅማቸው ውስን ስለነበረ በዋነኛነት የድምፅ አገልግሎት ብቻ ነበር የሚሠጡት፡፡ ከ600 ያነሠ መስመር ነበር የሚይዙት፡፡ አሁን ግን ሁሉም በፋይበር ተቀይረው የእስክሪፕቶ ቀፎ ስፋት መጠን ያለው ኬብል ከ10ሺህ በላይ መስመር የመያዝ አቅም አለው፡፡ እነዚህ ሁሉ በኤሌክትሪክ ነው የሚሠሩት። ተደጋጋሚ የሃይል መቆራረጥ በሚደርስበት ጊዜ አንደኛ አቅማቸው እየደከመ ነው የሚሄደው፡፡ ሃይል በሚቆራረጥበት ጊዜ ባትሪው አቅሙ እየደከመ ነው ይሄዳል፡፡ ሙሉ በሙሉ ሊቃጠልም ይችላል፡፡ ወደ መፍትሄው ስንመጣ፣ አንደኛ የፋይበር ኦፕቲክ መቆረጥን ለመታደግ በተለይ አለማቀፍ ግንኙነታችን ላይ ኢፒጂ ደብሊው የሚባል አለ በዚያ ነው እየዘረጋን ያለነው፡፡

ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን ጋር ስምምነት አድርገን ከፍተኛ የሃይል ጭነት በሚባለው የኤሌክትሪክ መስመር ላይ ነው ወደ ሞምባሣ እና ወደ ሌሎቹ አካባቢዎች የሚሄደውን መስመር እየዘረጋን ያለነው፡፡ ይህ ሲሆን በምንም መልክ ሊቆረጥ አይችልም፡፡ ከሦስት አመት በፊት በዓመት 34 የፋይበር ኦፕቲክ መቆረጥ ብቻ ነበር የሚደርሠው፡፡ አሁን ግን በወር ከ45 በላይ አንዳንዴም 60 ይደርሣል፡፡ ይሄ ማለት በአገልግሎት ጥራቱ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ አለው፡፡ ወደ ህጉ ከመጣን፣ አንዳንድ ሃገሮች ፋይበር ኦፕቲክ ለቆረጠ የሞት ቅጣት ፍርድን አስቀምጠዋል፡፡ በእነዚህ ሃገራት እንኳን ኬብል ቆርጦ አገልግሎት የሚያቋርጥ ቀርቶ በአጠገቡም የሚያልፍ የለም፡፡ በወር 45 ጊዜ የሚቆረጥበት ሃገር ከኢትዮጵያ በስተቀር የለም፡፡ አሁን እንደተቋም ሌላ መፍትሄ ብለን የያዝነው በአየር ሞገድ የሚሄድ ማይክሮዌቭ ማስተላለፊያ አለን፡፡

ይሄ በየትም በኩል ቢቆረጥ አገልግሎቱ አይቆምም፤ ነገር ግን መጨናነቅ ይፈጥራል፡፡ የኤሌክትሪክ መቆራረጥን እንደ ችግር ደጋግመው እያነሡልኝ ነው፡፡ ሁለቱ አካላት መ/ቤቶች ተነጋግራችሁ ችግሩን መፍታት አልተላችሁም ማለት ነው? በጋራ እየሠራን ነው፡፡ በተለይ በጣም መሠረታዊ የሚባሉ አገልግሎቶቻችን ላይ ከእነሡ ጋር እየሠራን ነው፡፡ እንደ ሃገር በሚደርሠው መቆራረጥ ነው እኛ ጀነሬተር፣ ባትሪ የመሣሠሉትን መፍትሄዎች የምንጠቀመው፡፡ ነገር ግን መሠረታዊ የሚባሉት ላይ ከእነሱ ጋር እየተመካከርን ነው፡፡ የመስመር ስልኮች በአብዛኛው አካባቢዎች ሲቋረጥ ደንበኞች ለመስሪያ ቤቱ ቢያመለክቱም መፍትሄ እንደማይሠጥ በርካቶች እንደስሞታ ያቀርባሉ፡፡ አገልግሎቱ የሚቆራረጥበት ምክንያት ምንድን ነው? ለምንድንስ ነው በፍጥነት ምላሽ የማይሠጠው?

በመሠረታዊነት ከመደበኛ የስልክ መስመር ጋር ተያይዘው የሚታዩ ችግሮች አሉ፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ በጣልያን ጊዜ የተዘረጋ የኮፐር ኬብል ነበር። አሁን እያጋጠመ ያለው መሠረታዊ ችግር ከተማዋ እያደገች ያለች ነች፡፡ ከመንገድ እና ከልማት ስራዎች ጋር በተያያዘ የኬብል መቆራረጥ ይከሠታል፡፡ ሁለተኛ ደግሞ የማይግሬሽን ስራም እየተሠራ ነው፤ ማለትም ድሮ ከነበረበት ወደ አዲሱ (ከመዳብ ወደ መልቲ ሠርቨር ኬብል ጌትዌይ) እየተሸጋገረ ነው፡፡ ከማዛወሩ ጋር ተያይዞ የሚታዩ ችግሮች አሉ፡፡ የአንዳንዶቹ ያለ መግባት፣ የመሣት የመሣሠሉ ችግሮች አሉ፡፡ ከጥገና ጋር ተያያዞ የተነሣው ማንኛውም ደንበኛ ብልሽት ሲያጋጥመው በስልክ ደውሎ ያስመዘግባል፡፡ ከዚያ ቲቲ ቁጥር (Travel ticket Number) ይሠጠዋል፡፡ ከተቀበሉ በኋላ በየዞኑ በየአካባቢው ላሉ አካባቢዎች ተላልፈው፣ እዚያ ያሉ ባለሙያዎች እንዲሠሩት ይደረጋል፡፡ ይሄ ሲባል ግን ችግር አያጋጥምም ማለት አይደለም፤ ያጋጥማል፡፡

ነገር ግን ችግር የደረሠባቸው ተጠቃሚዎች ወደ ተቋሙ ቀርበው በአካል ቢያመለክቱ መልካም ይሆናል፡፡ በአጠቃላይ ግን የተንቀሣቃሽ፣ የኢንተርኔት እንዲሁም የመደበኛ ስልክን በተመለከተ ተቋሙ ጥራትን መሠረት አድርጐ ሊሠራ እየተንቀሣቀሠ ነው፡፡ ወደ 26 ፕሮጀክቶች ተቀርፀዋል፡፡ እስካሁን ትልቁ ትኩረት የነበረው መሰረተ ልማቱን የመዘርጋት ነበር፡፡ አሁን ግን ወደ ጥናት መሄዱ ትኩረት ተደርጐበታል፡፡ በየሣምንቱ ይህን በተመለከተ ስራ አስፈፃሚው ተሠብስቦ ይገመግማል፡፡ በተለይ ከመደበኛ የመስመር ስልኮች ጋር የሚታዩ ችግሮች ይኖራሉ፡፡ በተቋሙም እነዚህ ችግሮች ይታወቃሉ፡፡ ግን ችግራቸው ለብዙ ጊዜ የዘለቀባቸው ወደ ተቋሙ ቢመጡ የማስተካከል እርምጃ ይወሠዳል፡፡ በአጠቃላይ ግን የተቋሙ ዋነኛ እቅድ በዚህ አመት መጨረሻ ላይ 40 ሚሊዮን የሞባይል ተጠቃሚ እንዲኖር ማድረግ ነው፡፡ አሁን 22 ሚሊዮን ነው ያለነው፡፡ አፈፃፀሙን ካየነው በ2003 እና በ2004 ከእቅዱ በላይ ነው ያሣካው። በሞባይል አገልግሎት አሁን ከአፍሪካ በ6ኛ ደረጃ ላይ ነው ያለነው፡፡ ከአራት ዓመት በፊት 13ኛ ነበርን፣ የዛሬ ሁለት ዓመት ደግሞ 9ኛ ሆንን፣ ዓምና 6ኛ ሆነናል፡፡ ኬንያን ቀድመን ማለት ነው፡፡

ከአፍሪካ እኛን የሚደቀድሙን ናይጄሪያ፣ ግብፅ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ሞሮኮ እና አልጄሪያ ናቸው፡፡ የአንድ ሃገር የቴሌኮም ልማት የሚለካው በሃገሪቱ ያለው የቴሌኮም ቁጥር ለህዝቡ ሲካፈል በሚገኘው ውጤት ነው፡፡ በዚህ ደረጃ እኛ ፔኔትሬሽን ሬታችን ወደ 28 በመቶ ደርሷል፡፡ ከ20 አመት በፊት 0.25 በመቶ ነበር አሁን 25 በመቶ ደርሠናል፡፡ በቀጣይ ሁለት አመት ደግሞ ከእጥፍ በላይ ለማድረስ ነው ጥረት የሚደረገው፡፡ ሠራተኞቻችሁ የሰዎችን የስልክ ጥሪ ልውውጥ ሚስጥር ለሰው ያሳያሉ ይባላል? ይህን ማድረግ ይቻላል? በመሠረቱ የኛ ተቋም የስልክ ንግግርን አይቀዳም። እኛ ያለን ተጠቃሚው የደወለበት (Call detail record) ዝርዝር ነው፡፡ አንድ ተጠቃሚ መቼ፣ በስንት ሰአት፣ የት ደወለ የሚለው ነው ያለን፡፡ ከዚህ ውጪ የመልዕክቱን ፍሬ ሃሳብ የሚመዘግብም መሣሪያ የለንም፡፡ በስልክ የተለያዩ ወንጀሎቹ ይሠራሉ፡፡ ለምሣሌ ዛቻ ሲፈፀም ፖሊስ በምርመራ ሲጠይቃችሁ ኮምፒውተር ውስጥ የለም፤ አልተመዘገበም ይባላል። ለምንድን ነው? ከዚህ ጋር በተያያዘ ማንኛውም ተጠቃሚ ዛቻ እና የመሳሰሉት ሲደርሱበት በመጀመሪያ ለፖሊስ ያሳውቃል፡፡ ፖሊስ በምን ስልክ ነው የደረሰብህ ይላል።

ከዚያም ወደ ተቋማችን መጥቶ ፖሊስ የሚጠይቀው አንደኛ በዚህ ቁጥር ላይ ያለው ማን ነው? ሁለተኛ ደግሞ ያደረገውን ልውውጥ ሪከርድ ነው፡፡ ይህ ሲሆን ነው አልተመዘገበም የሚባለው። አሁን ሲምካርድ እየተሸጠ ያለው በተለያዩ የግል አቅራቢዎች ነው። በመሠረታዊነት በደንቡ እያንዳንዱ ሲም ካርድ አከፋፋይ በሚሸጥበት ጊዜ የእያንዳንዱን ገዢ ሙሉ አድራሻ መያዝ አለበት፣ አድራሻ ሳይዝ ከሸጠ እሱ ነው ተጠያቂ፣ ያ አድራሻው ሳይያዝ የተሸጠለት ግለሰብ ወንጀል ቢሠራና ፖሊስ መረጃውን ቢጠይቅ እኛ ጋር ስለማይመዘገብ አድራሻው ኮምፒውተር ውስጥ የለም ማለት ነው፡፡ ይህን ተገንዝቦ ማንኛውም አከፋፋይ የሚሸጥለትን ሰው ሙሉ አድራሻ በሚገባ መያዝ አለበት፡፡ በሞባይል ለተጠቃሚዎች ከእናንተ ተቋም እና ከሌሎች የንግድ ድርጅቶች የሚላኩ አጭር መልዕክቶች የሰዎችን ፍላጐት የጠበቁ አይደሉም፣ የሰአት ገደብ ስለሌላቸውም ሌሊት ሳይቀር መልዕክቶቹ ይላካሉ ተጠቃሚውንም ይረብሻሉ፣ ተቋሙ ይሄን ነገር እንዴት ነው የሚያየው? እስካሁን ይሄንን አሠራር አቅጣጫ የሚያሳይ አዋጅ አልነበረም፤ አሁን ግን አዋጅ አለ፡፡ የብሮድካስት አዋጅ ላይ በትክክል ተቀምጧል፡፡

ወደ ስራ ሲገባ በቀጣይ እያንዳንዱ ተጠቃሚ አስቀድሞ ማስታወቂያ ትፈልጋለህ ወይ ተብሎ መጠየቅ ይኖርበታል፡፡ አዎ እፈልጋለሁ ብሎ ከላከ ይላክለታል፡፡ አልፈልግም ካለም አይላክለትም። ይህን ለመከታተል የብሮድካስት ባለስልጣንም አለ፤ ኢትዮቴሌኮምም ባለድርሻ ነው። በቀጣይ ወደተግባራዊ ስራው ለመግባት ባለድርሻ አካላቱ እየተወያዩበት ነው፡፡ መልዕክቶቻችሁ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ነው የሚተላለፉት፡፡ ምን ያህል ደንበኛ በአግባቡ ይረዳናል ብላችሁ ታስባላችሁ? በመሠረታዊነት እኛ ሀገር ያሉ ቀፎዎች አማርኛን የሚቀበሉ አይደሉም፡፡ አብዛኛው በእንግሊዝኛ ነው። በዚህ ደግሞ እኛም እየተቸገርን ነው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን የሃገር ውስጥ ቋንቋን ታሳቢ የሚያደርጉ እየመጡ ነው፡፡ በኛ ሃገር አሁን ባለው ከኢንተርኔት ከ80 በመቶ በላይ የመረጃ የምንቀዳው (Download) በሌላ ቋንቋ ነው፡፡ እኛ በሀገር ቤት ቋንቋ የምንጭነው መረጃ የለንም፡፡ እኛ ቢሆንልን በሁሉም ቋንቋዎች መላክ እንፈልጋለን፡፡ ነገር ግን ይሄን የሚያስተናግድ ቀፎ ተጠቃሚ ጋር የለም፡፡ አሁን ያሉት የሃገር ውስጥ ቋንቋ ቀፎዎች ከ1 በመቶ በታች ናቸው፡፡

“ምን ገበያ አለ…ዝም ብሎ ብሩን መብላት እኮ ነው?”

የአራት ልጆች እናት ለሆኑት ለወ/ሮ ሮማን ታደሰ አመት በዓላት የጭንቀት፣ የሃሣብና፣ የሰቀቀን ጊዜያቶች ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ውስጥ ተቀጥረው የተጣራ 1170 ብር ወርሃዊ ደመወዝ የሚከፈላቸው ባለቤታቸው በየወሩ የሚሰጧቸውን አንድ ሺህ ብር አብቃቅተው ወር ለመድረስ ሁሌም ጭንቅ ነው፡፡ ከቀበሌ ተከራይተው ላለፉት 28 ዓመታት የኖሩባትን ቤት በወር 37 ብር ይከፍሉባታል፡፡ ከወር አስቤዛ፣ ከቤት ኪራይ፣ ከውሃና መብራት ክፍያ ተርፎ በእጃቸው የሚቀር ቤሣቤስቲን ኖሮአቸው አያውቅም፡፡ ሁሉም ልጆቻቸው የሚማሩት በመንግስት ትምህርት ቤቶች ውስጥ ነው፡፡ እንዲህ እንደ አሁኑ አመት በዓል በመጣ ቁጥር የወ/ሮ ሮማን ትልቁ ጭንቀት “ምኑን ከምኑ አብቃቃዋለሁ” የሚለው ጉዳይ ነው፡፡

በመቶና በመቶ ሃምሣ ብር ቅርጫ ተገብቶ ዘንቢል ሙሉ ሥጋ ወደ ቤት በሚመጣበት፣ በሃያና በሃያ አምስት ብር ወሠራ ዶሮ በሚገዛበት በዚያ በደግ ዘመን ከጐረቤቶቻቸው ጋር ምሣና እራት እየተጠራሩ አመት በዓልን በደስታ ሲያከብሩት ኖረዋል፡፡ ጊዜ አያመጣው የለ እንዲሉ ሆነና ዶሮ 200 ብር ዋጋ ስታወጣ፣ አንድ ኪሎ ሥጋ 180 ብር ሲሸጥ ዕድሜ ቁጭ አድርጐ አሣያቸው፡፡ ወ/ሮ ሮማንን ያገኘኋቸው መርካቶ ዶሮ ተራ ውስጥ ነው፡፡ ከወር ወጪያቸው ላይ ለአመት በዓል መዋያ ቀንሰው በመሃረባቸው ቋጥረው የያዟትን አራት መቶ ብር ከጉያቸው ወሽቀዋታል፡፡ ከቅቤ ተራ ዶሮ ተራ፣ ከዶሮ ተራ ሽንኩርት ተራ ሲንከራተቱ ውለው የሰሙት ዋጋ ናላቸውን አዙሮታል፡፡ ኪሎ ሽንኩርት ዘጠኝ ብር መሆኑን ጠይቀው ተረዱና ቅቤ ተራ ገቡ፡፡

አንዱን ኪሎ ለጋ ቅቤ 180 ብር ብሎ ያስደነገጣቸውን ቅቤ ነጋዴ በልባቸው እየተራገሙ ባዶ ዘንቢላቸውን አንጠልጥለው ዶሮ ተራ ገቡ፡፡ ትርምሱና ጫጫታው በዶሮ ተራ የባሰ ነው፡፡ ምናለሽ ተራን አካቶ ምዕራብ ሆቴል ድረስ ባለው ሥፍራ ላይ የዶሮ ንግዱ ተጣጡፏል፡፡ ገዥና ሻጭ ይነታረካል። አይናቸው የገባውን ዶሮ አነሱና ዋጋውን ጠየቁ፡፡ ነጋዴው ዶሮውን ተቀብሎአቸው በእጁ መዘን መዘን አደረገውና መቶ ዘጠና ብር አላቸው፡፡ ደነገጡ። አንድ ዶሮ 190 ብር? ቅቤውስ? … ሽንኩርቱስ? ዳቦውስ? … አንዷ ሁለት ብር ከሰባ ሳንቲም ዋጋ የወጣላት የእንቁላሏስ ጉዳይ? ግራ ገባቸው፡፡ በመሀረብ ተቋጥራ በጉያቸው ያለችውን 400 ብር በልባቸው ማደላደል ያዙ፡፡ ገንዘቧ ከአንድ ኪሎ ቅቤና ከአንድ ዶሮ በላይ ለመግዛት አቅም የላትም። ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ አመት በዓላት ለእሣቸው የጭንቀትና የሰቀቀን ጊዜያት እየሆኑባቸው ቢሄዱም የዘንድሮው የባሰ ሆነባቸው፡፡ ጭንቀታቸውን የሚረዳ፣ ችግራቸውን የሚካፈል ሰው ከጐናቸው አለመኖሩ አሣዘናቸው፡፡

ባለቤታቸው “አብቃቅተሽ መዋል ነው እንጂ ምን ይደርጋል” ማበካከን?! ከማለት የዘለለ መፍትሔ የላቸውም፡፡ ህፃናት ልጆቻቸው ጐረቤቶቻቸው ቤት ስለተገዛው ዶሮና በራፋቸው ላይ ስላሠሩት በግ እያወሩ “የእኛስ የታለ በማለት ሥቃያቸውን ያበዙባቸዋል፡፡ ምን ይሻለኛል? … ከበርካታ ሰዓታት ሃሣብና ጭንቀት በኋላ ግማሹን ኪሎ ቅቤ ዘጠና ብር፣ አነስ ያለውን ዶሮ በ165 ብር፣ 5 ኪሎ ሽንኩርት በ45 ብር ሂሣብ ገዙ፡፡ ዘንቢላቸው 300 ብር ወጪ ያደረጉባቸውን ዕቃዎች ሸክፋ ይዛለች፡፡ ወ/ሮ ሮማን የመርካቶውን ዶሮ ተራ ለቀው ከመውጣታቸው በፊት አግኝቼ ገበያው እንዴት ነበር አልኳቸው፡፡ “ተይኝ ልጄ ምን ገበያ አለ… ዝም ብሎ ብሩን መብላት እኮ ነው፡፡ አሁንማ በዓል የሚባለው ነገር ባይመጣብኝ ደስታዬ ነው። አመት በዓላት የመደሰቻና ከወዳጅ ዘመድ ጋር የመገባበዣ ጊዜያት የነበሩበት ያ ወርቅ ዘመን አልፏል፡፡ ያኔ አመት በዓልን … በዓል አስመስለነው ውለናል፤ ደግሰን አብልተናል፤ ከጐረቤቶቻችን እየተጠራራን እንኳን አደረሳችሁ ተባብለናል… አበቃ … የዛሬው ዝም ነው፡፡ ይህቺ ዘንቢል እንኳን ስንቱን አይታለች፡፡

ለሸክም የሚከብድ ቅርጫ ሥጋ እንዳልገባበት ዛሬ ወፍ የምታህል ዶሮ ተሸክማለች … ተይኝ ልጄ” ምሬታቸውን ተነፈሱ፡፡ መልካም በዓል እንዲሆንላቸው ተመኝቼ ተሰናበትኳቸውና የገበያተኛዋን እናት የገበያ ውሎ ቅኝቴን ቀጠልኩ። በግምት 10 ዓመት የሚሆነውን ወንድ ልጃቸውን አስከትለው ገበያ ከወጡ አንዲት እናት ላይ አይኔ አረፈ፡፡ ወ/ሮ ዘውድነሽ ተክሉ ይባላሉ። ለበዓል ገበያው ከቤታቸው የወጡት ማለዳ ላይ ቢሆንም ገና ሸመታቸውን አላጠናቀቁም፡፡ ለበዓሉ ያስፈልጉኛል ያሏቸውን ነገሮች ለመግዛት አስበው ከቤታቸው ይዘው የወጡት ገንዘብ እንደሃሣባቸው ሊያደርግላቸው ባለመቻሉ ተጨንቀዋል፡፡ “በዓመት በዓል ምድር ልጆቼ የሰው ቤት አያዩም” በሚል ከባለቤታቸው ጋር ሲሟገቱ አምሽተው የሰጧቸው ገንዘብ ገና በዶሮና ሽንኩርቱ ገበያ ወገቤን ብላለች። ቀሪውን ጉዳይ እንዴት ብለው፣ ከምን አምጥተው እንደሚያሟሉ ግራ ገብቷቸዋል፡፡ እንደ ወ/ሮ ሮማን ሁሉ ለወ/ሮ ዘውድነሽም የበዓላት ወቅቶች የጭንቅና የሃሳብ ጊዜያት ናቸው፡፡ ከቤት ሥራ አንስቶ የበዓል ዝግጅቱ፣ ሸመታው፣ ገንዘብን አብቃቅቶ ሁሉን ሸማምቶ ለመመለስ የሚደረገው ጭንቀት … “ውይ በዓልስ ባልመጣ” የሚያሰኝ ሆኖባቸዋል። “አሁንማ እንኳን አደረሰሽ ሲሉኝ ብልጭ እያለብኝ ነው፡፡

የሚያሾፉብኝ፣ የሚቀልዱብኝና እኔን ለማናደድ የሚሉኝ ሁሉ ይመስለኛል፡፡ ቆይ የት ነው የምደርሰው? እንኳን ለበዓሉ አደረሰሽ ከሚሉኝ እንኳን ለጭንቅ ሰሞን አደረሰሽ ቢሉኝ ይሻለኛል፡፡ ከአንደኛው በዓል ቀጣዩ ከቀጣዩ ደግሞ መጪው የከፋ እየሆነብኝ የልጆቼንና የቤተሰቤን ደስታ ፍለጋ እኳትናለሁ፡፡ ለገና በ120 ብር ዶሮ ገዛሁ እያልኩ ስማረር ይኸው ለፋሲካ 200 ብር ገብቶ ቆየኝ፡፡ ከየት አምጥቼ ነው የምገዛው፡፡ ልጆች እንደው ችግር አይገባቸው፡፡ በጓደኞቻቸው ቤት የሚደረገውን የሚገዛውን እያዩ ይሳቀቃሉ፡፡ መቼም ህይወቴ እያለች ልጆቼ በበዓላት የጐረቤት ደጃፍ አይረግጡብኝም፡፡” እልህና ብሶት ከገፅታቸው ላይ የሚታይባቸው እኚህ እናት፤ የቀረው ይቅር ብለው ለበዓሉ ያስፈልገኛል ያሉትን ሁሉ ሸማምተው ወደ ቤታቸው እንደሚሄዱም ነግረውኛል፡፡ በመርካቶው የበዓል ገበያ ውስጥ አግኝቼ ያነጋገርኳቸው እነዚህ ሁለት እናቶች የአብዛኛውን ኢትዮጵያዊ እናት ብሶትና ጭንቀት ሊወክል የሚችል ሃሣብ እንዳላቸው በፒያሣው አትክልት ተራና በሰሜን ሆቴሉ የሾላ ገበያ ያገኘኋቸው እናቶች አረጋግጠውልኛል፡፡

`ከዓመታት በፊት 300 ብር ይዘሽ ገበያ ከወጣሽ የፍላጐትሽን ሸምተሽ ትመለሻለሽ፡፡ ዛሬ 300 ብር ሁለት ኪሎ ቅቤ እንኳን አትገዛም፡፡ ታዲያ እንዴት ሆኖ ነው ዓመት በዓል የሚከበረው?’’ ይላሉ - ገበያኛ እናቶችን፡፡ የሁሉም ገበያተኛ እናቶች ጭንቀት “ምኑን ከምን አድርጌው ላብቃቃው” የሚል ነው፡፡ ይህንን የእናቶች ጭንቀት የቤት አባወራዎችስ ምን ያህል ይካፈሏቸው ይሆን በሚል አቶ ስንታየሁ አክሊሉ የተባሉ አባወራን ጠየክኋቸው፡፡ “በበዓል ወቅት ለቤት አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን ለማሟላት አባወራውም የሚችለውን ያደርጋል፡፡ ያው እንግዲህ አቅሙ የፈቀደለትን ከማድረግና ያለውን ከመስጠት ሌላ ምንም ሊያደርግ አይችልም፡፡ ያለውን አብቃቅቶ እንደ ጊዜውና እንደ አቅም በዓሉን በዓል ማድረግ ደግሞ የሚስት ፋንታ ነው፡፡ አቶ ስንታየሁ ያላቸውን ገንዘብ ለሚስታቸው ከመስጠት ሌላ በበዓል ሸመታውና በእንዴት አድርጌ ላብቃቃው ጭንቀት ውስጥ የሉበትም፡፡

ያለውን አብቃቅቶ ማደርማ የሚስት ፋንታ ነው፡፡ አመት በዓል በመጣ ቁጥር ቅድምያ በሚሰጠው የሆድ ጉዳይ እናቶች ከማንም በላይ ጫና አለባቸው። በዓል በደንብ ካልተበላበትና ካልተጠጣበት ምኑን በዓል ሆነው?” የሚል እምነት ያላቸውን አባወራዎቻችና “እኛስ ቤት ለምን አይገዛም” እያሉ ቁምስቅል የሚያሣዩ ልጆቻቸውን ፍላጐት ለማሟላት ላይ ታች እያሉ በጭንቀት ይባትላሉ፡፡ የእነሱ ገቢ በዛው ባለበት ላይ ቆሞ እያለ የገበያው ዋጋ ከዕለት ዕለት መጨመሩ ለእናቶቹ ጭንቅ ሆኖባቸዋል። “አሁንማ አመት በዓል ይሉ ነገር ባልመጣብን” ብለው እስኪማረሩም አድርሷቸዋል፡፡

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

እንኳን ለብርሀነ ትንሳኤው በሰላም አደረሳችሁማ! ያው ‘ኔትወርክ’ እንደተለመደው በበዓል ሰሞን እንደልብ ስለማይሠራ ‘መልካም የትንሳኤ በዓል’ የሚል ‘ቴክስ ሜሴጅ’ ለሁሉም መላኬ ይመዝገብልኝማ! ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…አንዳንዴ ሳስበው ይሄ ‘ኔትወርክ’ የሚባል ነገር ልክ የሰው ባህሪይ ይዞ የሚያሾፍብን ይመስለኛል፡፡ ልክ ነዋ… አጠገብ ለአጠገብ ቆማችሁ ስትደዋወሉ… “ይቅርታ የደወሉላቸውን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም…” ምናምን የሚል ነገር ስትሰሙ የምር አስቸጋሪ ነው፡፡ ነው…ወይስ ይሄ እንደ አንዳንድ ከማዳን ይልቅ በሽታ ያብሳሉ እንደሚባሉት ከውጪ የሚመጡ መድሀኒቶች ለእኛ የሚለቀቀው ቴክኖሎጂ ‘ከማዳን የሚያብስ ነው!’ ልክ ነዋ…ቴክኖሎጂ እንዲህ በተራቀቀበት ዘመን ጎን ለጎን ሆነን እንኳን “…ማግኘት አይችሉም…” ነገር ስንባል…አለ አይደል… የሰዉ አንሶን ቴክኖሎጂም ያሹፍብን ብንል አይበዛብንም! “ኸረ እባክሽ አንቺ ሴትዮ ጎን ለጎን ነው የቆመነው!” ምናምን ለማለት አስቸጋሪ ሆነብንና…አለ አይደል… እንዲሁ ‘የገበጣ ጠጠር’ ሆነን ቀረን፡፡

በቃ…የገበጣ ጠጠር ባንከባለሉት በኩል መንከባለል ነው እንጂ ‘ኮምፕሌይንት’ ‘ፔቲሽን’ ቅብጥርስዮ ምናምን ነገር የለማ! እናላችሁ… አጠገብ ለአጠገብ ሆነን እንኳን “የደወሉላቸውን ማግኘት አይችሉም…” አይነት ነገር እነዚህ አፍ፣ ጆሮዎችና ዓይኖቻቸውን እንደሸፈኑት ጦጣዎች ምስል እየሆንን ነው፡፡ የምንናገረው ነገር እንደየሰዉ አተረጓጎም ሆኖ ‘የተደወለላቸው አልገኝ’ እያሉ ችግር እየሆነ ነው፡፡ “…የደወሉላቸውን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም…” በሁሉም ነገር እያየነው ነው፡፡ ለምሳሌ “አበበ በሶ በላ…” አለ አይደል…በቃ ጣጣ የለውም፣ “አበበ በሶ በላ…” ማለት ነው፡፡ በዚህ ዘመን ግን እያንዳንዳችን የየራሳችንን መዝገበ ቃላት ፈጠርንና ግንኙነታችን ሁሉ ‘የባቤል ግንብ’ ታሪክ አይነት እየሆነ ነው፡፡ የምር… ለምሳሌ አንዱ የእኔ ቢጤ “አበበ በሶ በላ…” የሚለውን የዓረፍተ ነገር አወቃቀር መማሪያ…“አበበ ካልጠፋ ምግብ ለምን በሶ እንዲበላ ተደረገ?” የሚል ሙግት ሊጀምር ይችላል፡፡ “ኧረ እባክህ ይሄ የአረፍተ ነገር አሰካክ መማሪያ እንጂ…” ብላችሁ ሳትጨርሱ “የፈለገ ዓረፍተ ነገር አሰካክ መማሪያ ቢሆንስ! ለምንድንው በሶ የሚሰጡት! ለምን አበበ ብርንዶ በላ አይባልም?” ብሎ አፍ አፋችሁን ሊላችሁ ይችላል፡፡ ደግሞላችሁ… “ጨቡዴ ጩቤ ጨበጠ…” በቃ ጨቡዴ ጩቤ ጨበጠ ማለት ነው — የአረፍተ ነገር አሰካክ መማሪያ፡፡

ዘንድሮ ግን የጨቡዴ ጩቤ መጨበጥ እንዲህ በቀላሉ የሚታለፍ ነገር አይደለም። ልክ ነዋ…“ካልጠፋ ነገር አበበ በሶ እየበላ፣ ጨቡዴን ጩቤ ማስጨበጥ ጨቡዴ ማፊያ ነው ለማለት ነው!” ምናምን የሚሉት አይነት ‘የደወሉላቸውን’ ሰው የማጣት ነገር አለላችሁ፡፡ ስብሰባ ተቀምጠን (‘ተኝተን’ ላለማለት ነው) የሚያበቃበት ሰዓት እንደ ‘ሚሊኒየሙ ግብ’ ርቆብን እያለ…አለ አይደል… ሰብሳቢው ምን ይላል መሰላችሁ…“በእውነቱ የተካፋዮች ንቃት የሚያስደስት ነው…” ኧረ በህግ አምላክ! (በነገራችን ላይ “በህግ አምላክ” ማለት ትልቅ የመብት ማስከበሪያ የነበረበት ዘመን እዚቹ እኛ አገር ውስጥ ነበር፡፡ የእውነት!) እናላችሁ… እኛ ጠቅላላ ‘ቫሊየም ፋይቭ’ እንደዋጠ ሰው እያንጎላጀጀን እያየ፣ ስለ ‘ንቃታችን’ ሲያወራ…አለ አይደል… አጠገብ ለአጠገብ ሆነን ‘የደወልንላቸውን ሰዎች’ ማግኘት እያቃተን ነው፡፡ ስብሰባ ላይ ከማንጎላጀጅ የባሰ ምን አይነት መደወል ይኖራል፡፡

ይቺን ስሙኝማ…በኮሚኒስት ሩስያ የኬጂቢ ጆሮ ጠቢ የሆነ ሰው ወደ አለቆቹ ይሄድና “ጎረቤቶቼ ከምዕራባውያን ጋር ግንኙነት አላቸው ብዬ እጠረጥራለሁ” ሲል ሪፖርት ያቀርባል፡፡ አለቃውም “በምን አወቅህ?” ሲል ይጠይቀዋል። ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው… “በየቀኑ እራታቸውን ይበላሉዋ!” እኔ የምለው…ካነሳነው አይቀር፣ የኮንዶሚኒየም ነዋሪ ወዳጆቼ እንደሚነግሩኝ ከሆነ…“በየቀኑ እራታቸውን ይበላሉዋ!” አይነት ‘ጆሮ በግድግዳ’ ነገር በሽ፣ በሽ ነው አሉ፡፡ እኔ የምለው… ከአኗኗር ጋር እኮ መለወጥ ያለባቸው አንዳንድ ባህሪያት አሉ አይደል እንዴ! የአፓርትማ ኑሮ እኮ… (ኮንዶሚኒየም ማለትም ያው አፓርትማ ማለት ነው…) የ‘ፕራይቬሲ’ ኑሮ ነው፡፡ (ስሙኝማ…ግድግዳ ላይ የተለጠፈ ጆሮ እንዳይሰማን ንግግራችንን በጽሁፍ መለዋወጥ እንችላለን፡፡ ይቺ ቁና፣ ቁና ትንፋሿስ! በቃላት አትጻፍ ነገር! ቂ…ቂ…ቂ… ጥያቄ አለን፣ ቀጥለው በሚሠሩ ኮንዶሚኒየሞች ‘ሳውንድ ፕሩፍ ቤድሩም’ ይሠራልን!) እናላችሁ…ምን ያደርጋል አንዳንድ ነገር…አለ አይደል… ሳያቀስ እንደማይለቀው ያዳቆነ ‘ሉሲፈር’ ነክሶ ይይዝና አይለቅም፡፡

እናላችሁ… ከሳፋና ከድስታችን ጋር የሰፈር አዋዋል ያልተጻፉ ‘ፕሪንሲፕሎቻችንም’ ተከትለውን ፎቅ ላይ ይወጣሉ፡፡ ልክ ነዋ…ቅድመ-ኮንዶሚኒየም እኮ… አለ አይደል… ላይ ሰፈር ያለነው ታች ሰፈር ስላለችው እንትናዬ “ምን አግኝታ ነው ዛሬ እንዲህ ያማረባት!” አይነት ነገር እንላለን፡፡ ታች ሰፈር ያሉት እነእንትና ደግሞ ላይ ሰፈር ያለነውን … “ትናንት ሥጋ ወጥ ሲሸተን ነበር፣ ዛሬ ደግሞ ቋንጣ ፍርፍር…ይሄ ሁሉ ሥጋ ከየት እየመጣ ነው!” ሊሉን ይችላሉ። እናላችሁ…ይሄ ይሄ ተከትሎን ፎቅ ላይ እየወጣ ችግር እየሆነብን ነው፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…የኮንዶሚኒየም ነገር ካነሳን አይቀር አንድ ወዳጄ ያጫወተኝን ስሙኝማ… (ወዳጄ፣ ባለማስፈቀዴ ሂሴን ውጫለሁ…)…እሱና እሷ ኮንዶሚኒየም ሦስተኛ ፎቅ ላይ ይኖራሉ፡፡ እናላችሁ… አየሩ ፀሀያማ ከሆነ መስኮቱን ከፍተው ወደየሥራቸውና ወደየጉዳያቸው ይሄዳሉ፡፡ ታዲያላችሁ… ቴሌቪዥኑ የተቀመጠው መስኮቱ አጠገብ ነው፡፡ አንድ ቀን ታዲያ እነሱ በሌሉበት ዝናብ ይመጣና ወጨፎው ቴሌቪዥኑን ያረጥበዋል፡፡

ሰውየው ተናዶ… “ለምንድነው መስኮቱን ሳትዘጊው የሄድሽው!” ምናምን ብሎ ይጮህባታል፡፡ እሷም ምን ብትል ጥሩ ነው… “እኔ ምን ላድርግ፣ ሬዲዮ ነው ያሳሳተኝ!” ትላለች፡፡ ለምን መሰላችሁ… ለካስ ጠዋት የአየር ጠባይ ትንበያው ላይ “ዛሬ አዲስ አበባ ከፊል ደመናማ ሆና ትውላለች…” ተብሎ ነበር። አሪፍ አይደል! ልክ ነዋ… ቢያንስ በአየር ጠባይ ትንበያ መሠረት የሚንቀሳቀስ ሰው መኖሩን ማወቅም አሪፍ ነው፡፡ እናላችሁ…ዘንድሮ “…የደወሉላቸውን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም…” ነገር በየቦታው ያልተጻፈ መመሪያ አይነት ነገር ሆኖላችኋል፡፡ ስሙኝማ…ጋብሮቮዎች ሁለት ጊዜ ያልባቸዋል ይባላል፡፡ አንድ ጊዜ ፀሀይ ሲበዛባቸውና ሌላ ጊዜ ደግሞ ገበያ ሄደው ዋጋ ሲከራከሩ፡፡ እኛ አለን እንጂ… ‘እንትን በሚያሳቅፈው’ ብርድ ሁለት መቶ ሁለት ጊዜ የሚያልበን! ለምን አትሉኝም… በየሄድንበት ‘የደወልንላቸውን ማግኘት’ እያቃተን! ለክፉም ለደጉም በዚህ በበዓል ሰሞን የደወልንላቸውን እንዳናገኝ የሚደነቀሩ ደንቃራዎችን አንድዬ ከመንገዳችን ላይ ዘወር ያድርግልንማ! ስሙኝማ…በዛ ሰሞን በበሬ ሥጋ ውስጥ የፈረስ ሥጋ እየቀላቀሉ ሸጡ ምናምን ተብሎ አውሮፓ ታምሶ ነበር፡፡ ለነገሩ ግርግሩ ለምን ቀላቀሉብን ነው እንጂ ፈረሱንም፣ በሬውንም ስልቅጥ አድርገው ነው የሚበሉት፡፡

(እኔ የምለው…እነሱ እኮ የምግብ እጥረት የማይገጥማቸው…አለ አይደል… በመሬት የሚሄደውም፣ በሰማይ የሚበረውም፣ በባህር የሚዋኘውም አንዱም ሳይቀራቸው “እነሆ በረከት” ስለሚሉ ነው! አሀ.. እኛ ‘ቋቅ’ ሲለንስ! አይደለም… የምድር ላይ ተሳቢ ምናምን ‘አውሬ’ ሥጋ፣ አሁንም እኮ ፓስታ ‘ቋቅ’ የሚላቸው የገጠር ሰዎች መአት ናቸው!) እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ፣ ይቺን ስሙኝማ…የፈረንጁ ልኳንዳ ነጋዴ የፈረስ ሥጋ ከሌላ ሥጋ ጋር ቀላቅሎ ሲሸጥ ተገኘና ፍርድ ቤት ቀረበ፡፡ ዳኛው “ህዝቡ ሳያውቅ የፈረስ ሥጋ በመሸጥ ተከሰሃል፣ ምን መልስ አለህ?” ይሉታል፡፡ እሱ ሆዬም ምን ይላል…“ክቡር ዳኛ፣ ለነገሩ የፈረስ ሥጋ ብቻ አይደለም የሸጥኩት፡፡ ግማሽ የፈረስ ሥጋና ግማሽ የጥንቸል ሥጋ እየቀላቀልኩ ነው የሸጥኩት፡፡” ዳኛውም… “ጥሩ፣ ለመሆኑ ለአንድ ፈረስ ስንት ጥንቸል ቀላቀልክ?” ሲሉት እሱ ምን ቢል ጥሩ ነው… “ክቡር ዳኛ፤ ግማሸ ለግማሽ አልኩ እኮ፣ ማለት አንድ ፈረስ ለአንድ ጥንቸል፡፡” አሪፍ አይደል! ስሙኝማ… ለነገሩ ጊዜያችን የማይታሰቡ ነገሮች ሁሉ የሚሠሩበት ስለሆነ የምትሸምቱትን ሥጋ በደንብ እያያችሁ ግዙማ! ሁሉም ነገር በልክ ቢሆን አሪፍ ነው፡፡ የሁሉንም ነገሮች ‘ትንሳኤ’ ያፋጥንልንማ! መልካም የበዓል ሰሞን ይሁንላችሁማ! ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

የአስገድዶ መድፈር ወንጀል ለተፈጸመባቸው ሴቶች የህክምና ማስረጃ መስጠት እና በመረ ጃው የህግ ተጠቃሚነት ምን ይመስላል በሚል ዶ/ር ብርሀኑ ከበደ ያደረጉት አንድ ጥናት እን ደሚጠቁመው አስገድዶ መድፈር የወሲብ ጥቃትን ማድረስ እንደመሆኑ ለስነተዋልዶ ጤና መጉ ዋደል የሚያደርስ ነው፡፡ ዶ/ር ብርሀኑ ጥናቱን ያደረጉት በአዲስ አበባ በተለያዩ ክፍለከ ከተማ ዎች ሲሆን ለናሙና ጥናት የተመረጡትም ወደ 244 የሚሆኑ ሰዎች ናቸው፡፡

አዲስ አበባ 10 ክፍለከተማዎች ያሉዋት ሲሆን የህዝቡዋም ቁጥር 2739551 እንደሚደርሰ በ2007 እንደአው ሮፓውያኑ አቆጣጠር የተደረገ ጥናት ያስረዳል፡፡ በጥናት ወረቀቱ ላይ እንደተመለከተው ፡- 44 በመቶ የሚሆኑ ሴቶች በሕይወት ዘመናቸው የወሲብ ጥቃት ይፈጸመባቸዋል፡፡ ከአምስት ሴቶች አንዱዋ በ21 አመት እድሜ ለዚህ ጥቃት ልትጋለጥ እንደምትችል ያስረዳል፡፡ በወሲብ ከተጠቁት ሴቶች መንከል 50 በመቶ ያህል ለህግ ሪፖርት የተደረገላቸወ ናቸው፡፡

ምንም አንኩዋን በተናጠል የሚወሰድ እርምጃ ወደ ውጤት የማያደርስ ቢሆንም ጥቃቱን ያደረሱ ሰዎች በህግ እርምጃ ሲወሰድባቸው ተጎጂዎቹ እንደሚረኩ ሁኔታዎች ያስረዳሉ፡፡ የወሲብ ጥቃት ከደረሰባቸው ከ10-30 በመቶ የሚደርሱት ሴቶች ጉዳይ በህግ ሽፋን ተሰጥቶታል፡፡ ተገዶ መደፈር በሚያጋጥምበት ጊዜ ከህግ ክፍሎች ለሚቀርበው ጥያቄ የህክምና ማስረጃ መስጠት ግድ ሲሆን ከዚህም ባለፈ በአንል ቀርቦ የማስረዳት ግዴታም ከህክምናው ባለሙያ ይጠበቃል፡፡ የወሲብ ጥቃት የተፈጸመባቸው ሴቶች የሚደርስባቸው ጉዳት አንላዊ ብቻ ሳይሆን ስነልቡናዊና አእምሮአዊ ችግርም ሊደርስባቸው ይችላል፡፡ ነገር ግን ጥቃት አድራሹ በህግ ፊት ቀርቦ የጥፋቱን ያህል ብይን ሲያገኝ ማየት ለተጠቂዎቹ እርንታን እንደሚሰጥ አያጠራጥርም፡፡

በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በሌሎችም አገሮች እንደሚታየው ተገደው ለተደፈሩ ሴቶች የሚሰጠወ የህክምና ማስረጃ ብዙ ጊዜ አጠያያቂ የሚሆንት አጋጣሚ ይስተዋላል፡፡ በተለይም ጥቃቱ የተፈጸመባቸው ሕጻናት ሲሆኑ በፍጥነት መረጃውን ወደሐኪም የሚያደርሰው ሰው ስለማይኖር በመታጠብ እንዲሁም ቀናትን በመቁጠር ምክንያት ሊታይ የሚገባው መረጃ ስለሚጠፋ ለፖሊስ የሚሰጠው ምላሽ የቆየ የሚል ይሆናል፡፡ በዚህም ምክንያት ቤተሰብም ሆነ የህግ ክፍሉ ግልጽ የሆነ ምላሽን ስለማያገኙ ለውሳኔው እንደሚቸገሩ እሙን ነው፡፡ ነገር ግን የወንድ የዘር ፈሳሽ ከአቸውም ይሁን ከልብሳቸው ላይ ሳይጠፋ የደፈረው ሰው ማን እንደሆነ ሊታወቅ ይችላል፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

የፋሲካ አመጋገባችን እንዴት ነው?

ተልባ የጨጓራን መላጥ ይከላከላል በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ ከፍተኛ ግምት ከሚሰጣቸው በዓላት አንዱ በሆነው የፋሲካ በዓል ዋዜማ ላይ እንገኛለን፡፡ በዓሉ ከአምሣ አምስት ቀናት ፆም በኋላ የሚከበር በአል እንደ መሆኑ አከባበሩም ከሌሎቹ በዓላት ለየት ባለ መልኩ ነው፡፡ አንጀታችን ለሁለት ወራት ገደማ በቅባትና በሥጋ ላይ ማዕቀብ ጥሎ እንደመክረሙ፣ በዕለተ ፋሲካ ድንገተኛ ለውጥ ሲደረግበት ሊቆጣ ወይም ተግባሩን ለመፈፀም ፈቃደኛ ላይሆን ይችላል፡፡ በዚህ የተነሳም በደስታ ልናከብረው ያሰብነውን በዓል በጭንቀትና በህመም ልናሣልፈው እንችላለን፡፡

ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የተገኘ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በበዓላት ሰሞን ወደተለያዩ ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎች ለህክምና ከሚመጡ ታካሚዎች መካከል አብዛኛውን ቁጥር የሚወስዱት ከበዓል አመጋገብ ጋር በተያያዝ በሚከሰቱ የአንጀትና የጨጓራ ችግሮች ጉዳት የደረሰባቸው ህሙማንና ከአልኮል መጠጥ ጋር በተገናኙ የተለያዩ ችግሮች ሣቢያ ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች ናቸው፡፡ የምግብ አለመፈጨት ችግር በተለያዩ ጊዜያትና በልዩ ልዩ ምክንያቶች የሚከሰት ችግር ቢሆንም በበዓላት ሰሞን ችግሩ ሰፋ ብሎ ይታያል፡፡ ይህ የሆነበትን ምክንያት የውስጥ ደዌ ስፔሻሊስት የሆኑት ዶ/ር ምህረት ተስፋው ሲናገሩ፤ “በበዓላት ቀናት አመጋገባችን ከወትሮው በተለየ ሁኔታ በመሆኑና ቅባትና በርበሬ የበዛባቸዉን ምግቦች አብዝተን የምንመገብ ስለሆነ እንዲሁም በአንድ ጊዜ በርካታ ምግቦችን ስለምንመገብ ነው፡፡

ከዚህ በተጨማሪ አልኮልና ቡና አብዝቶ መጠጣት፣ ጭንቀት፣ የጣፊያ መቆጣትና በሆድ ዕቃ ውስጥ የአየር መከማቸት፣ የምግብ አለመፈጨት ችግርን ከሚያስከትሉ ጉዳዮች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ የምግብ አለመፈጨት ችግር መኖሩን ከሚጠቁሙ ምልክቶች መካከል የሆድ መነፋት፣ የሆድ ህመም፣ ቃር፣ የአየር መብዛት፣ ማቅለሽለሽና ማስመለስ፣ ጨጓራ አካባቢ የሚሰማ የህመም ስሜትና፣ ግሣት ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ እኒህም በታማሚው ላይ ጭንቀትና ከባድ የህመም ስሜትን ሊፈጥሩ ይችላሉ፡፡ በበዓላት ወቅት የሚኖረንን የአመጋገብ ባህርይ ተከትሎ የሚከሰተውን የምግብ አለመፈጨት ችግር ለመፍታት ዋንኛ መፍትሔ ይሆናል ያሉትን ጉዳዮች ዶ/ር ምህረት እንዲህ ይዘረዝሯቸዋል፡፡ “በተለይ እንዲህ እንደ አሁኑ አንጀታችን ከሥጋና ከቅባት ምግቦች ለወራት ታቅቦ ከቆየ በኋላ፣ ሣናለማምደው በድንገት ቅባትና በርበሬ የበዛባቸውን ምግቦች ስንመገብ ህመሙ በቀላሉ ሊፈጠር ይችላል፡፡

ስለዚህም ቅባት የበዛባቸዉን ምግቦች በተቻለ መጠን መቀነስ፣ በአንድ ጊዜ ብዙ አለመመገብ፣ ቀበቶን አጥብቆ አለማሰር የምግብ መፍጨት ሥርዓቱ የተስተካከለና ጤናማ እንዲሆን ያግዛል፡፡ “የምግብ አለመፈጨት ችግርን ያግዛሉ ተብለው በህክምናው ዘርፍ ከሚታመንባቸው መድሃኒቶች ይልቅ ከላይ በዝርዝር የተገለፁት ነገሮች ችግሩ እንዳይከሰት፣ ከተከሰተም ለከፋ ችግር እንዳይዳርግ ሊከላከሉ የሚችሉ ናቸውና አዘውትረን ልንጠቀምባቸው ይገባል” ዶክተር ምህረት ይመክራሉ፡፡ በፆም ፍቺ ወቅት ቅባት ነክ ምግቦችን ከመመገባቸው ወቅት አንዳንድ ሰዎች ተልባ ወይንም አብሽ ይጠጣሉ፡፡ ይህም ጨጓራቸው የሚሰጠውን ምግብ በአግባቡ ለመፍጨት እንዲችል ለማዘጋጀት እንደሚረዳቸውም ይናገራሉ፡፡ ይህንን ጉዳይ አስመልክተው ዶክተር ምህረት ሲናገሩ፤ “ነገሩ በአብዛኛው ህብረተሰብ ዘንድ የተለመደና ተዘውትሮ የሚፈፀም ጉዳይ ነው፡፡

በህክምናው ረገድም ጠቀሜታ ያለው ነገር እንደሆነም ይታመናል፡፡ በተለይ ተልባ በውስጡ የሚዝለገለግ ነገር ስላለውና ይህ ዝልግልግ ነገር በጨጓራው ውስጠኛው ክፍል ገብቶ መላጥ እንዳያስከትል ይከላከላል” ብለዋል፡፡ ሌላው ከበዓላት ጋር ተያይዞ የሚከሰተው የጤና እክል ደግሞ አልኮል አብዝቶ በመጠጣት የሚፈጠር ችግር ሲሆን እንደ ፋሲካ ባሉ ታላላቅ በዓላት የአልኮል መጠጥ በአብዛኛው ህብረተሰብ ዘንድ የተለመደ በመሆኑ አልኮል በጨጓራ ላይ የሚፈጥረው ተጽዕኖ የማቅለሽለሽ ስሜት እንደሚፈጥር ባለሙያው ያስረዳሉ፡፡ ጉበት አልኮሉን ለማብላላት በሚያካሂደው እንቅስቃሴ የደም ስኳሩ መጠን ስለሚቀንስ በግለሰቡ ላይ የድካም ስሜት እንዲፈጠርና ሰውነቱ እንዲዝል ያደርገዋል፡፡

አልኮል አብዝተው የጠጡ ሰዎች ራስ ምታት፣ አፍ መድረቅ፣ ድካም፣ ትኩሣት፣ ማስመለስና ተቅማጥ ሊያጋጥማቸው ይችላል። ይህ ችግር ያጋጠማቸው ሰዎች ውሃ አብዝተው በመጠጣት ናርኮቲክ መድሃኒቶችን በመውሰድና በቂ እረፍት በማድረግ ችግራቸውን ሊያስወግዱ እንደሚችሉ ዶ/ር ምህረት ይገልፃሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ብዙ መጠጥ ጠጥተው ይህ አይነት ችግር ሲገጥማቸው ከህክምናው ይልቅ ተለምዶአዊ በሆነው ዘዴ ችግራቸውን ለማስወገድ ጥረት ሲያደርጉ ይታያሉ፡፡ ከእነዚህ መካከልም የቲማቲም ጭማቂ መጠጣት፣ የሽሮ ፍትፍት መመገብና ውሃ አብዝቶ መጠጣት በህክምናው ዘርፍም የሚደገፍ ሲሆን ችግሩን ለማስወገድ ይረዳል እየተባለ የሚወሰደው ተጨማሪ የአልኮል መጠጥ ችግሩን ከማባባስ የዘለለ መፍትሔ እንደሌለው ባለሙያው ይገልፃሉ፡፡ መጪውን በዓል በሠላም፣ በጤናና በደስታ እናከብረው ዘንድ ጤናችንን ከሚያጓድሉ ችግሮች መጠበቅ ግድ ይለናል፡፡ መልካም በዓል ይሁንልን!!

Published in ዋናው ጤና

“ምርጫዎች ቀን ቆጥረው ይመጣሉ፤ ውጤቱን እንዲለውጡ ግን አንፈልግም”

ሶሻሊስቶች ለህዝብ ጥቅም በሚል ሰበብ በሥልጣን ላይ ለመቆየት የሚሹት በዲሞክራሲያዊ መንገድ አይደለም፡፡ በዚህም ሳቢያ ፍትሃዊ ምርጫ ማድረግ አይዋጥላቸውም፡፡ ተፈጥሯዊ ባህርያቸውም አይደለም፡፡ የእነሱ ዝነኛ ብሂል “የትም ፍጪው [ስልጣኑን] አምጭው” የሚል ነው፡፡ ከጊዜ ወደ ጊዜ በአገራችን በሚካሄዱ ምርጫዎች፣ ምርጫ ቦርድና አስፈጻሚዎቹ ለምርጫ ሕጎችና አሰራሮች አልፎ ተርፎም ለመርሆዎች ተገዢ አለመሆናቸውና ለጉዳዩ ትኩረት መንፈጋቸው ሳያንስ፣ ገዢው ፓርቲ በገሃድ “ተቃዋሚዎች መጡም አልመጡም ግድ የለንም” እስከማለት መድረሱ ለመድብለ ፓርቲ ስርዓት ፈታኝ ጥያቄ ነው፡፡ የምርጫ ቦርድና የአስፈጻሚዎቹ ትኩረት፣ አማራጭ ሃሳቦች አብብው ሕዝብ በአማራጭ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ እንዲኖረው ማገዝ ሳይሆን እንደ ዓመታዊ በዓል ቀን ቆጥሮ ምርጫውን በማንኛውም ኪሳራ(At any cost) ውስጥ ማስፈፀም እየሆነ የመጣ ይመስላል ፡፡

ይህ አካሄድ የሚጠቁመን ነገር ቢኖር ከጊዜ ወደ ጊዜ ስር እየሰደደ የመጣው ሃቀኛ ዴሞክራሲ ሳይሆን የመንግስታዊ ከበርቴና የልማታዊ መንግስታት አስተሳሰብ መሰረት የሆነው የተምሳሌታዊ ዴሞክራሲ መሆኑን ነው፡፡ መጀመርያ ተቃዋሚዎችን ከነአቤቱታቸው በማስወገድ፣ ቀጥሎ በምርጫው አካሄድና ወግ አልባነት የተቆጣውን መራጭ ሕዝብ፣ ከቁጣው ለማብረድና እምነቱን በተጽእኖ ለማስለወጥ፣ ቤት ለቤት በሚያደርጉት መጠነ ሰፊ ፕሮፓጋንዳና ወከባ ማስጨነቃቸው፣ የፈለጉት የሕዝቡን “የይስሙላ ተሳትፎ” እንጂ ውጤት የማስለወጥ ሕጋዊ መብቱን እንዳልሆነ አይተናል፡፡ ልማታዊ መንግስታት፣ በዴሞክራሲያዊ ምርጫ የመሸነፍና የለውጥ ጥያቄ እንዲነሳባቸው አይፈቅዱም፡፡ ለዚህ ሲባልም የምርጫ ውድድር ቀንን ጠብቆ ምርጫ አለ ከማለትና ሕዝብ አማራጭ በሌለበት እንዲሳተፍ ከማዋከብ ውጭ ሌላ አማራጭ ሃሳብ እንዲጎለበትና እንዲያብብ እድል አይሰጡም፡፡

በእኛም አገር የገጠመን ይሄ ዓይነት ችግር ነው፡፡ የውይይትና ክርክር መድረኮች አሳታፊ፣ ሚዛናዊና ክፍት ሆነው ከውይይቱና ክርክሩ በሚገኙ ግብአቶች ላይ ተመርኩዞ፣ ሕዝብ ይሁንታውን እንዲሰጥ የሚያደርጉ ዴሞክራሲያዊ አሰራሮች ፈተና ገጥሟቸዋል፡፡ አሁን አሁን ደግሞ ምርጫ ቦርድና አስፈጻሚዎቹ ለመገናኛ ብዙሃን በሚሰጧቸው ዘገባዎች ላይ ማዳመጥ የጀመርነው ነገር ቢኖር፣ አማራጮች ይበቁናል ወይም ከዚህ በላይ አያስፈልጉም ፤ የሚሉ ሆነዋል፡፡ ይህ እንግዲህ በዘመናዊ አባባል ፤ ምርጫዎች ቀን ቆጥረው ይመጣሉ፤ ውጤቶቹን እንዲለውጡ ግን አንፈልግም፡፡ መራጭም ሆነ ተመራጭ ይህንኑ በቅድሚያ አምኖ ትርጉም በሌለው ምርጫ ከፈለገ ይሳተፍ፤ ካልፈለገ ይቅርበት የማለት ያህል ነው፡፡ ይህ እንግዲህ ለልማቱ የተመረጡ፣ የተሰጡ ወይም የተቀቡ ሰዎች ስላሉ፤ የሕዝብ ሚና መሳተፍ እንጂ ምርጫን መለወጥ እንዳልሆነ የሚያሳይ ድርጊት ነው፡፡

ወደ ኋላ የምመለስበት ጉዳይ ቢሆንም የዚህ አይነቶቹ ዝንባሌዎች በስፋት ለመስፈናቸው በቂ ምሳሌዎችን ማቅረብ ይቻላል፡፡ ጊዜው እጅግ ከረፈደና ለዝግጅት በማይመች ሁኔታ በወር ለአስር ደቂቃ ብቻ የተሰጠው የአየር ሰዓትን ሚዛናዊ ለማስመሰል የተቀነቀኑት ቀመሮችና ስሌቶች፤ ምን ያህል በ“ተጨፈኑ ላሞኛችሁ” የተሞሉና ብትፈልግ ተቀበል ወይም ተወው (Take it or leave it) በሚል ማን አለብኝነት የታጠሩ እንደነበረ መገመት ይቻላል፡፡ አማራጭ ሃሳቦች ቀርበው ተሳትፎው በራሱ ጊዜ እንዲደምቅ ከመስራት ይልቅ፤ በድራማ ላይ ማተኮር የተለመደ በመሆኑ ምርጫው በሕዝብ ዘንድ ተቀባይነትና ተአማኒነት የነበረው ለማስመሰል፤ መራጮች ተገደውም ቢሆን መውጣት አለባቸው እስከማለት በመደረሱም “እስኪ የመረጥክበትን ጣት አሳየን” በማለት የተፈጸሙት ማዋከቦችና ማስጨነቆች ሌሎቹ መገለጫዎች ናቸው፡፡ የምርጫው እንቅስቃሴ ሙሉ ለሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ በምርጫ ቦርድ ኃላፊነት የሚከናወን መሆኑ ቀርቶ፤ በቀበሌና በመሰረታዊ ድርጅቶች አማካኝነት ለእለት ጉርሳቸውም ሆነ ለኢኮኖሚያዊ ፍጆታቸው ሲባል በአንድ ለአምስት በተደራጁና በቀበሌ አስፈጻሚዎች እጅ መውደቁን ለመታዘብ ችለናል፡፡

ይህ ድርጊት የምርጫ ቦርድን ሕገ-መንግስታዊ ስራና ሚናውን የጨፈለቀ ከመሆኑም በላይ፣ ገና ከጠዋቱ በሕዝብ ዘንድ የምርጫውን ተአማኒነትና ተቀባይነት ፈጽሞ ያደበዘዘ ነበር፡፡ ምርጫው ከተጀመረበት እለት ጀምሮ “ሕዝብ በምርጫው ላይ በንቃት እንዲሳተፍ የማድረግ መብትና ግዴታ አለብን” በሚል ግልጽነት የጎደለው ሰበብ፤ በመደራጀትና በመሰባሰብ በዜጎች ላይ ልክ ያጣ ማዋከብና ማስገደድ ተፈጽሟል፡፡ የነዋሪነት መታወቂያ ካርድ ሳይጠየቅ የመራጮች ምዝገባ ተካሂዷል፡፡ የማህበራዊ አገልግሎት ተጠቃሚነትን ማስገደጃ በማድረግ፣ የነዋሪነት ስም ዝርዝር ተይዞ ቤት ለቤት በተደረገ ዘመቻ፤ የመምረጫ ካርድ መውሰድ ያልፈለጉ ዜጎች የምርጫ ካርድ በግድ እንዲወስዱ ተደርጓል፡፡ እጩ ምዝገባን በሚመለከት የተፈጠረውን የእጩ ክፍተት ለመሙላት፤ በተለያየ መንገድ በተቀነባበረ ስልት በፓርቲዎች እውቅና የሌላቸው ግለሰቦች በፓርቲዎች ስም እንዲመዘገቡ ተደርጓል፡፡ በምሳሌነት የሚነሳው በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ብሔራዊ ክልል ውስጥ በኢዴፓ እውቅና ያልተሰጣቸው፤ ነገር ግን የኢዴፓ እጩ ነን የሚሉ ግለሰቦች ያለ ፓርቲው የድጋፍ ደብዳቤና የአባልነት መታወቂያ እጩ ሆነው እንዲቀርቡ ተደርጓል፡፡

የምርጫው እለትም ምርጫው በሕዝብ ዘንድ ተቀባነት ያለውና የዜጎችን ይሁንታና ታማኝነት ያገኘ ለማስመሰል፣ ገና ጎሕ ከመቅደዱ ጀምሮ በአንድ ለአምስት የተደራጁ ሃይሎችን ወደ ምርጫ ጣቢያ እንዲተሙ በማድረግና ለዚሁ በተዘጋጁ የመገኛኛ ብዙሃን ተዋናዮች አማካኝነት ቪዲዮ በመቅረጽ፤ ምርጫውን ደማቅ ለማስመሰል ተሞክሯል፡፡ ቀኑ እየረፈደ ሲመጣና ዜጎች በምርጫው ለመሳተፍ ፍላጎት ማጣታቸውንና ወደ ምርጫ ጣቢያ እንዳልወጡ ሲታወቅ፣ በሞባይል ስልክ ጥሪ በማድረግ፣ መንገድ ላይ በመጠበቅና ቤት ለቤት በመዝመት፣ ሕዝብ ወደ ምርጫ ጣቢያ እንዲሄድ ተጽእኖ የታከለበት ከፍተኛ ውትወታ ተካሂዷል፡፡ በሳምንቱ እሁድም የነበረው የመራጩ ተሳትፎ ቁጥሩ በእጅጉ እንደሚመናመን ስለተገመተ ሕገ-መንግስታዊ መብታቸውን ተጠቅመው አንመርጥም ያሉትን ዜጎች፣ “የማትመርጡ ከሆነ የመምረጫ ካርዳችሁን መልሱ” በማለት ባላመኑበት ምርጫ ያለመሳተፍ ሕገ-መንግስታዊ መብታቸው ሲጣስ ተስተውሏል፡፡

ከላይ እንዳየነው መነሻው ኢ-ሞራላዊ በሆነ ተጽእኖ በአፈና፣ በወከባና በማስጨነቅ ለጊዜውም ቢሆን ሕዝብ ወደ ምርጫ ጣቢያ እንዲሄድ ማድረግ ችለዋል፡፡ ነገር ግን ሂደቱ ለውጤትና ለቆጠራ የሚበቃ የመምረጫ ወረቀት ከኮሮጆ ውስጥ ለማግኘት አልረዳቸውም፡፡ መጨረሻም ላይም ቆጠራው የተደረገው መራጮችን በማወዳደር አሸናፊውን ለመወሰን መሆኑ ቀርቶ፤ በምርጫ ኮሮጆ ውስጥ የሞላውን በብሶት፣ በቁጣና በምሬት የታጨቀ ሃተታ ሲያነቡ ለመዋል ተገደዋል፡፡ የምርጫውን ጉዳይ ከማሳረጌ በፊት በምርጫው ሰሞን የገጠሙኝን ጉዳዮች አንስቼ ጸሑፌን ላሳርግ፡፡ የምርጫውን ሂደት ለመታዘብ ተዘጋጅቼ ስለነበረ፣ የምርጫው ዕለት በአንድ በኩል የሸገር ኤፍ ኤምን የቀጥታ የምርጫ ዘገባ እያዳመጥኩ፣ በሌላ በኩል ደግሞ በርካታ የምርጫ ጣቢያዎችን እየተዘዋወርኩ ለመከታተል ችያለሁ፡፡ መንግስታዊ መገናኛ ብዙሃን በተደጋጋሚ ከሚያዘንቡት የዘጠና ዘጠኝ ፐርሰንት የሕዝብ ተሳትፎ በስተቀር ምልዕተ ሕዝቡም ሆነ እኔ በግሌ፣ የሸገር ኤፍ ኤም ዘጋቢዎችም በተናጠል መታዘብ የቻልነው እውነታ ቢኖር፣ ምርጫው ቀኑን ቆጥሮ ከመከናወኑ ውጭ፣ ሂደቱ በኢትዮጵያ የምርጫ ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ በመድብለ ፓርቲ አሳታፊነቱም ሆነ በመራጭ ሕዝብ ቁጥር ብዛት እጅግ ዝቅተኛ ሆኖ አልፏል፡፡

ሌላው በዚህ ምርጫ ላይ የታየውና ለምስክርነት የሚቀርበው ጉዳይ፣ በአስገዳጅ ሁኔታ ወደ ምርጫ ጣቢያ የወጣው ሕዝብ፤ የምርጫ ካርዱን በተለያየ መንገድ የተቃውሞ መግለጫው ሲያደርግ መዋሉ ነው፡፡ በምርጫው ቀን ሕዝቡን በነቂስ ለምርጫ እንዲያስወጡ ግዳጅ የተሰጣቸው የአንድ ለአምስት ሰራዊቶች፤ ሕጋዊም ሆነ ኢ-ሕጋዊ በሆነ መንገድ በማስጨነቅና በማዋከብ በርካታ መራጭ ወደ ጣቢያ ማስወጣት ችለዋል፡፡ ይህ አካሄዳቸው ባዶ ኮሮጆ ከማግኘት አድኗቸው ሊሆን ይችላል፡፡ ተገዶ የወጣው መራጭ ግን ለፈለጉት አላማ መሳርያ ሊሆን አልቻለም፡፡ በእምቢታው እንዳይፀና የደረሰበት ተጽእኖና እንግልት ቢያግደውም፣ ያለፍላጎቱ ወደ ምርጫ ጣቢያ መሄዱን እንደማይቀበል ጨዋነት በተሞላበት መንገድ ተቃውሞውን ገልጿል፡፡ መራጩ ሕዝብ ተገዶ በተገኘባቸው የምርጫ ጣቢዎች ላይ ነጻ ጋዜጦችን ያገኘ ይመስል በምርጫ ሰነዶች ላይ የብሶት ስሜቱን በመፃፍ ለቆጠራ የማያገለግሉ አድርጓቸዋል፡፡ ሌላው ትዝብቴ በማታው ኢቴቪ ዜና እወጃ ላይ ያዳመጥኩት ጉዳይ ነበር፡፡ በምሽቱ የሁለት ሰዓት ዜና እወጃ ላይ የተለያዩ ክልሎችን የምርጫ እንቅስቃሴ ዘገባ ካደመጥን በኋላ የአማራ ክልል ዘገባ ተከተለ፡፡ ዘጋቢው በአማራው ክልል ውስጥ የምርጫው እንቅስቃሴ አስደሳች እንደነበረ ከገለፀ በኋላ፣ በጠቅላላ በአማራ ክልል ለምርጫ ከተመዘገበው ዘጠኝ ሚሊዮን ሕዝብ መካከል ስድስት ሚሊዮኑ እንደመረጠ ገለፀ፡፡ ጆሮዬን ማመን አቃተኝ፡፡ ማመን ያዳገተኝ ቁጥሩ አልነበረም፡፡

ምርጫው የተጠናቀቀው ከረፋዱ አስራ ሁለት ሰዓት ላይ ሆኖ እያለ፣ ዘጋቢው ዜናውን ያቀረበው ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ላይ መሆኑ ነበር፡፡ ለመገመት እንደሚቻለው በመሃል ያለፈው ጊዜ ሁለት ሰዓት ብቻ ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ የስድስት ሚሊዮን መራጭ መረጃ አቀናብሮ መዘገብ መቻሉ እውነትም ምርጫ ቦርድ ዘምኗል የሚያስብል ነበር፡፡ እንግዲህ የአማራውን ክልል የቆዳ ስፋት፣ የምርጫ ጣቢያ ስብጥርና ብዛት ገምቱት፡፡ ከዚህ ሰፊ ቦታ የሚሰባሰበው የመራጭ መረጃ በስልክ ተጠናክሮ ቀረበ ቢባል እንኳ መረጃው ዜና ለመሆን እንደቦታው ርቀትና እንደ መረጃው ስፋት ቢያንስ አንድ ቀን አሊያም ሳምንታት ሊፈጅ እንደሚችል ለመገመት አያዳግትም፡፡ ዘጋቢው ግን ለዚህ ጉዳይ ደንታ አልነበረውም፡፡ ምርጫ ቦርድ በተለያየ ጊዜ የሰጣቸውን መግለጫዎችና ማብራሪያዎችን ለተከታተለው እንዲህም ማለትና ማድረግ ይቻላል እንዴ የሚያሰኙ ናቸው፡፡ በአንድ በኩል ለምርጫው ሃያ አንድ ፓርቲዎች እንደተመዘገቡ እየተለፈፈ፤ በሌላ በኩል ከሁለትና ከሶስት ያልበለጡ ፓርቲዎች ያቀረቧቸውን እጩዎች ስም መለጠፍና ማስተዋወቅ የመረጃ እጥረት ወይስ ምርጫን ለማድመቅ የተሰራ ፕሮፓጋንዳ የሚል ጥያቄ የሚያስነሳ ነው፡፡ በተለይ ደግሞ ምርጫን በነጻና ገለልተኛ መንፈስ፣ በሕጋዊ አሰራር ላይ ተመስርቶ ሁሉም ፓርቲዎች እንዲሳተፉበት ሁኔታዎችን ማመቻቸት ያለበት ምርጫ ቦርድ፤ የተዛባ መረጃ መስጠቱ አሳሳቢ ሂደት ነበር፡፡ ምርጫ ቦርድ አልፎ ተርፎ የተወዳዳሪ ፓርቲዎችን ቁጥር አዛብቶ በማቅረብ፣ ቀሪዎቹን ማጣጣል ለምን እንዳስፈለገው ፈፅሞ አይገባም፡፡

ምን አልባት የተቋቋመበትን ዓላማ መርሳት ሊሆን ይችላል፡፡ በለሆሳስ ሲባል የከረመው “ኢህአዴግ እስካለ ድረስ ሌላው ሃይል ቀረም መጣ የሚያመጣው ነገር የለም” የሚል ድምዳሜ ላይ ላለመደረሱስ ምን ማረጋገጫ ሊቀርብ ይችላል፡፡ ጉዳዩ አሳሳቢና መልስ የሚሻ ጥያቄ ነው፡፡ በመራጭች ምዝገባ ወቅትና በእጩ ማስመዝገብ ሂደት ላይ በተግባር የታዩ በተለይም ምርጫውን ጥርጣሬ ላይ የጣሉ ጉዳዮችን መፍታት የምርጫ ቦርድ ስራ ነው፡፡ በተለይም የምርጫን ውጤት ሊያዛቡ እንደሚችሉ የተገመቱ ግዴለሽነቶችን በመመርመር ለመታረም ከመዘጋጀት ይልቅ ጥያቄ ያነሱትን ፓርቲዎች ሐሰተኛ ማድረግ ለምን አስፈለገ? ምንም ይሁን ምን ለውድድር የቀረቡ ፓርቲዎች እስካሉ ድረስ ለቀሪዎቹ ጥያቄ ቦታ አልሰጥም ማለት የመድብለ ፓርቲ ስርዓትን በማዳከም ተጠያቂ ማድረጉ አይቀሬ ነው፡፡ ምርጫ ቦርድ ከተቋቋመበት መሰረታዊ ዓላማ መካከል ዋነኛው የፓርቲዎችን ተሳትፎ በማጎልበት ሕዝቡ አማራጭ ሃሳቦችን እንዲያገኝ ማገዝ ነው፡፡ በመቀጠልም ነጻና ገለልተኛ ምርጫ በማካሄድ፡፡ ሕዝብ የሚደግፈውን ፓርቲ እንዲመርጥ ሁኔታዎችን ማመቻቸት ነው፡፡ የሕዝብ የስልጣን ባለቤትነትም የሚረጋገጠው በዚህ መንገድ ብቻ ነው፡፡ በምርጫ ቦርድ ዘገባ መሰረት፣ ከተመዘገቡት 23 ፓርቲዎች በላይ 30 ፓርቲዎች ጥያቄ አለን እያሉ፤ ጥያቄያቸውን በማጣጣልና ሕዝብን አማራጭ በማሳጣት፣ ምርጫን ማካሄድ የትም የማያደርስ የዝግ መንገድ ጉዞ መሆኑ የምርጫ ቦርድ ቃል አቀባዮች ሊያጡት ባልተገባ ነበር ፡፡ አሁን አሁን የምርጫ ቦርድ ቃል አቀባዮች “ትልቅና ትንሽ የሚባል ፓርቲ የለም፡፡ ለኛ ሁሉም ፓርቲዎች እኩል ናቸው” ሲሉ ማዳመጥ የተለመደ ነው፡፡

ለፕሮፓጋንናዳ ፍጆታ ካልሆነ በስተቀር ፓርቲዎች ከምን አኳያ እኩል ሆኑ የሚል ጥያቄ ቢነሳ፣ የምርጫ ቦርድ ቃል አቀባዮች መልስ እንደሌላቸው ግልጽ ነው፡፡ ምክንያቱም ኢህአዴግ ለምርጫ ከሚደለደለው የመገናኛ ብዙሃን የአየር ሰዓት ውስጥ ሰባ በመቶውን፣ በመንግስት ከሚመደበው የገንዘብ ድጎማ መካከል የአንበሳውን ድርሻ ሲወስድ ትልቅና ትንሽ ከሚል መስፈርት ውጭ ምንም ዓይነት የክፍፍል ቀመር እንዳልነበር “የአዋጁን በጆሮ” ነው፡፡ ይህም ሆኖ በዚህ ሁሉ ውጣ ውረድ ውስጥ አልፈው ለምርጫ የተዘጋጁ ፓርቲዎች ቁጥሩ ከሚወዳደሩት በላይ መሆኑ እየታወቀ፣ “ለመወዳደር የፈለጉ ፓርቲዎች እስካሉ ድረስ ችግር የለብኝም” በሚል ስሌት ምርጫን ያህል ነገር ማካሄዱ፤ ምርጫው “ኢህአዴግ እስካለ ድረስ ሌላ ምን ያስፈልጋል” ወደሚል ድምዳሜ ሊገፋ እንደሚችል ጠቋሚ ነው፡፡ ልማታዊ መንግስት መጀመርያውንም ቢሆን ፓርቲዎችን አዳክሞ “ተወዳዳሪ ስለጠፋ ምን ማድረግ ይቻላል፤ ምርጫው ባለው ተሳታፊ መቀጠል አለበት” ማለቱ የተለመደ ስልቱ ነው፡፡ በዚህ ኢ-ዴሞክራሲያዊ ስሌት ከቀጠልን የመድብለ ፓርቲና ዴሞክራሲያዊ ስርዓታችን ከአውራ ፓርቲ ወደ አንድ ፓርቲ ስርዓት እየተሸጋገረ ላለመሆኑ ከምርጫ ቦርድ ውጭ ማን ማረጋገጫ ሊሰጥ ይችላል፡፡ ምርጫ ቦርድ ይህ እንዳይሆን የተቋቋመ ዴሞክራሲዊ ተቋም መሆኑን መዘንጋቱ ግን ከሁለም በላይ አሳሳቢ ጉዳይ ነው፡፡

ዴሞክራሲያዊ ተቋማት ይህ ካልተከሰተላቸው ሂደቱ መልስ የሚጠይቀው ለፓርቲዎች ሕልውና ሳይሆን ቅድሚያ ለመድብለ ፓርቲ ስርዓት ሲሆን ቀጥሎ ተቋማቱ ለተቋቋሙበት ሕገ-መንግስት መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ እንደ ማጠቃለያ በዚህ ምርጫ ሂደት የተጐሳቆለውና የታመመው ሌላ ሳይሆን በማቆጥቆጥ ላይ የነበረው የመድብለ ፓርቲ ስርዓታችንና የሕዝብ የስልጣን ባለቤትነት ነው፡፡ በእኔ እምነት በምርጫ የመወዳደርና ያለመወዳደር እሰጥ አገባ የፈጠረው ተግዳሮት በማንም አሸናፊነት አልተጠናቀቀም፡፡ ሊጠናቀቅም አይችልም፡፡ ተቃዋሚዎች በአቅማችንና በልካችን ወንበር አሸንፈን የመድበለ ፓርቲ ስርዓቱን ለማጠናከርም ሆነ አማራጭ ሆኖ ለመቅረብ የነበረንን እድል የነፈገ ምርጫ ነበር፡፡

ኢህአዴግ የተሰዋለትና የተዋደቀለት የመድብለ ፓርቲ ስርዓት፤ አማራጭ ሃሳቦችን በቅጡ ማስተናገድ አልቻለም፡፡ የዴሞክራሲ ተቋማትም ይህንን አጣብቂኝ ለመፍታት የሚያስችል ሃቀኛነት፣ ብቃት፣ ተነሳሽነትና ተቆርቋሪነት ማሳየት አልቻሉም፡፡ በመጨረሻም ሂደቱ የተጠናቀቀው ሕዝብ በምርጫ ስርዓትና በመድብለ ፓርቲ ፖለቲካችን ላይ ስጋት እንዳደረበት ነወ፡፡ ሕዝብ አማራጭ በሌለበትና ውድድር በደበዘዘበት የምርጫ ሂደት ውስጥ ሆኖ የስልጣን ባለቤትነቱን በተግባር ማየትም ሆነ ማሳየት አልቻለም፡፡ ማብቂያ ከሌለው አጣብቂኝ እንወጣ ዘንድ ቆም ብለን እንድናስብ ጊዜው የግድ ይላል፡፡

ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነኝ የተከበሩ አቶ ስብሃት ነጋ (አቦይ ስብሃት) በሳምንታዊው አዲስ አድማስ ጋዜጣ የሚያዝያ 12 ቀን 2005 ዓ.ም እትም ላይ የሰጡት ቃለ ምልልስ ነው፡፡ የተቃዋሚ ፓርቲ ከፍተኛ አመራር፣ እንዲሁም የፓርላማ አባል በነበርኩበት ወቅት ከበርካታ የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር የመገናኘት እድል ነበረኝ፡፡ አልፎ አልፎ ፓርላማ ብቅ ሲሉ በቅርብ ርቀት ከመመልከት ውጪ ከአቶ ስብሃት ጋር ግን ተገናኝቼ አላውቅም፡፡ ይሁን እንጂ፣ እርሳቸው በተለያዩ አጋጣሚዎች የሰጧቸውን ቃለ ምልልሶች ከጋዜጦችና ከመጽሔቶች ላይ አንብቤአለሁ:: ከሬዲዮና ከቴሌቪዥን ተከታትያለሁ፡፡ በአንዳንድ ጋዜጦች ላይ በስማቸው የጻፏቸውን ሃሳቦችም ያነበብኩበት ጊዜ አለ፡፡ ከእነዚህ መረጃዎች የተገነዘብኩት ነገር ቢኖር፤ አቶ ስብሃት መሰረቱ የፀና አቋም ያላቸው፣ በፖለቲካ ጉዳይ የጠለቀ ግንዛቤና እውቀት ባለቤት መሆናቸውን ነው፡፡ አቶ ስብሃት እንደ ሀገራችን ፖለቲከኞች (በተለይ በተቃዋሚው ጎራ እንዳሉት) መያዣ መጨበጫ የሌለውና በመረጃ ያልተደገፈ አሉባልታ አይናገሩም፡፡

ትናንት የተናገሩትን ዘንግተው እንደመጣላቸው አይቀባጥሩም። (ለዚህም ልዩ አክብሮት አለኝ) እናም፣ ወደ መድረክ ብቅ ባሉ ቁጥር የሚያቀርቧቸው ሃሳቦች (አንዳንዶቹን የማልስማማባቸው ቢሆኑም) ግልጽ እና ቀጥተኛ በመሆናቸው እጅግ ይገርሙኛል፣ ይማርኩኛል፡፡ አቶ ስብሃት፤ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በሰጡት ቃለ ምልልስ በሰነዘሯቸው ሃሳቦች በበርካታዎቹ መቶ በመቶ እስማማለሁ። በአንዳንዶቹ ላይ ግን ስለማልስማማ ያለኝን የመከራከሪያ ሃሳብ እንደሚከተለው አቀርባለሁ፡፡ በዋናነት ትኩረት የማደርገው ክቡር አቶ ስብሃት ታጋይ ሰማዕታትን እና የባህር በርን አስመልከቶ በሰነዘሩት ሃሳብ ላይ ይሆናል፡፡ ጋዜጣው ቀዳሚ አድርጎ ያቀረበላቸው ጥያቄ “… 54 ሺህ ሰማዕታት እያሉ እንዴት ለአቶ መለስ ብቻ ተለይቶ ፋውንዴሽን ይቋቋማል የሚሉ ወገኖች አሉና የእርስዎ ምላሽ ምንድነው?” የሚል ነበር፡፡ በግሌ ለአቶ መለስ ፋውንዴሽን በመቋቋሙ እጅግ እጅግ ደስተኛ ነኝ፡፡ አቶ መለስ ኢትዮጵያን በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ ሳይንስን መሰረት ባደረገ መርህና በእውቀት ላይ ተመስርተው የመሰረቱና የመሩ ሰው ናቸው፡፡

እናም ይህ ፋውንዴሼን በስማቸው መቋቋሙ ቅሬታ የሚያስነሳ ሊሆን አይችልም። ይሁን እንጂ፣ የትጥቅ ትግሉ ዘመን ሰማዕታት ጉዳይ ሲነሳ፣ ሁልጊዜም የሚቆጨኝና እንደ እግር እሳት የሚያንገበግበኝ ነገር አለ፡፡ ይህንን ቁጭቴን ይበልጥ መሪር ያደረገው ደግሞ አቦይ የሰጡት መልስ ነው። “… 54 ሺህ ሰማዕታት [ያልከው] ምናልባት የትግራይ ሰማዕታት ብቻ ነው ሊሆኑ የሚችሉት…” ነበር ያሉት፡፡ ሻዕቢያ በትጥቅ ትግሉ ወቅት የተሰው ታጋዮቹን ብዛት ብቻ ሳይሆን የእያንዳንዱን ሰማዕት ስም፣ የተሰዋበትን ቦታ፣ ቀንና ሰዓት ጭምር መዝግቦ ይዟል ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ በአሳዛኝ መልኩ፣ አቦይ ከወጣትነት እስከ ጎምቱ ሽማግሌነታቸው ድረስ አባል በሆኑበትና በአመራርነት ጭምር ባገለገሉበት በሕወሓት/ኢህአዴግ ውስጥ በታጋይነት ተሳትፈው፣ የተሰው ሰማዕታትን ቁጥር እንኳ በትክክል ምን ያህል እንደሆነ አያውቁትም፡፡ አቦይ! እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ እኮ የእነዚህ ሰማዕታት አደራ አለበት።

እኔ ዛሬ ስፈልግ ተቃዋሚ ሆኜ፣ ስፈልግ ተራ ዜጋ ሆኜ ያሻኝን መናገር፣ መጻፍ፣… የቻልኩት እነዚያ ውድ የኢትዮጵያ ልጆች ውድ ሕይወታቸውን ገብረው በተፈጠረው መድረክ ነው፡፡ ሻዕቢያ የተሟላ ዝርዝር መረጃ ሲያዘጋጅ፣እኛ ምን ያህል እንደሞቱብን እንኳ በትክክል አለማወቃችን በቁም መሞታችንን ያመላክት እንደሆነ እንጂ ሌላ ምንም ሊሰኝ አይችልም፡፡ በሀገራችን ለአስራ ሰባት ዓመታት የተካሄደው የትጥቅ ትግል፣ አሁን ላለንበትና ወደፊትም ለምንደርስበት ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ሁኔታዎች ዋነኛ መሰረት በመሆኑ፣ በሀገራችን ታሪክ ሁነኛ ስፍራ ሊሰጠው እንደሚገባ አምናለሁ፡፡ እናም ይህ ታሪክ እንደ ቀዳሚዎቹ አነታራኪና አከራካሪ “የታሪክ ድርሳናት” አጨቃጫቂ እንዳይሆን በሀቀኛ መረጃዎች ላይ ተመስርቶ መሰናዳት ይኖርበታል፡፡ አፈሩን ገለባ ያድርግላቸውና አቶ መለስ ዜናዊ፣ ሰሜን ወሎ ቆቦ አካባቢ በተደረገ ጦርነት፣ ደርግ ያጠረውን ፈንጂ ተንከባለው የጠረጉ ሰማዕታት እንደነበሩ ደጋግመው ሲጠቅሱ ሰምቻለሁ። ለመሆኑ እነዚያ ሰማዕታት እነማን ናቸው? (ስማቸው፣ ዕድሜአቸው፣ አድራሻቸው፣…) ስንት ናቸው? ምን ያህል ወንድ? ምን ያህል ሴት? ይህ የሆነው መቼ ነው? (ቀን፣ ሰዓት፣ ዓመት) ቆቦ በየትኛው ጎጥ? እነዚያ ሰማዕታት ያን ኃላፊነት እንዴት ሊወስዱ ቻሉ? በወቅቱ ምን ተናገሩ?.... እነዚያ ሰማዕታት ያን ጀብድ ለመፈጸም ሲወስኑ ምንም አልተጨነቁ ይሆናል።

እኔ ግን እንዲህ ያለው ታሪክ በአግባቡ ተሰናድቶ ባለመቀመጡ ይጨንቀኛል፡፡ ይቆጨኛልም፡፡ ሰዎች ለታሪክ ምን ያህል እንደሚጨነቁ ለማሳየት ያህል ተጨማሪ ምሳሌዎችን ላቅርብ። ከወራት በፊት በአሜሪካ ሀገር በአንድ ት/ቤት ውስጥ አንድ ደመ-ነውጠኛ የከተማ ሽፍታ በከፈተው የተኩስ እሩምታ፣ ሃያ ሕፃናት እና ስድስት የትምህርት ቤቱ መምህራንና ሰራተኞች ሞቱ። ፕሬዝዳንት ኦባማ ለነዚህ “ሰማዕታት” በተደረገ የመታሰቢያ ሥነ-ስርዓት ላይ፣ የእያንዳንዱን ሟች ስም መጥራታቸውን አስታውሳለሁ፡፡ የሟቾችን ስም፣ ዕድሜ፣ ፎቶግራፍ፣ ወዘተ. የያዘ ሰሌዳም ተዘጋጅቷል፡፡ እስራኤላውያን በሂትለር የተጨፈጨፉ ዜጎቻቸውን መዝግበው መያዛቸውን፤ ሰርቦች፣ ክሮአቶችና በአጠቃላይ ዩጎዝላቪያውያን በእርስ በርስ ጦርነት ያለቁ ወገኖቻቸውን፣… በታሪክ መዝገብ ላይ አስፍረው መያዛቸውንም ሰምቻለሁ። እኛ ግን ግዙፍ የታሪካችን አካል የሆነ ተግባር የፈጸሙ ዜጎቻችንን ስም ዝርዝር ቀርቶ ብዛታቸውን እንኳ በቅጡ አናውቀውም፡፡ እነሱስ በጀግንነት ነው የተሰውት፣ እኛ ግን የቁም ሙት ሆነናል! - በአሳዛኝ መልኩ!!! በበኩሌ የመለስ ፋውንዴሽን በእርሳቸው ስራዎች እና የህይወት ታሪክ ላይ ብቻ ሳይታጠር በትጥቅ ትግሉ ወቅት የተሰው ሰማዕታትን ጉዳይ ጭምር እንዲያካትት ኃላፊነት ሊሰጠው ይገባል የሚል እምነት አለኝ፡፡ በዚህ ረገድ በግሌ ባለኝ እውቀት፣ ልምድና ችሎታ ማንኛውንም ነፃ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ለመስጠት ዝግጁ መሆኔን በዚህ አጋጣሚ ለአቦይ ስብሃት ብቻ ሳይሆን ለሚመለከታችሁ ሁሉ ለመግለጽ እወዳለሁ።

(ሃሳቤ ተቀባይ አገኘም አላገኘ እንደ ዜጋ የህሊና እረፍት ይኖረኛል) ክቡር አቶ ስብሃት ሰማዕታቱም ቢሆኑ “አልተረሱም፡፡ በየክልሉ ሀውልት እየተሰራላቸው ነው፡፡ በመላ የኢትዮጵያ ሕዝብም ዘላለማዊ የሕዝባዊነት ኃይል መልእክት እያስተላለፉ ይኖራሉ” የሚል ሃሳብም በዚሁ ቃለ ምልልሳቸው ገልጸዋል፡፡ ለሰማእታቱ የመታሰቢያ ሐውልት መሰራቱ መልካም ነው፡፡ “አልተረሱም” በሚለው የአቦይ ሃሳብ ሙሉ ለሙሉ ለመስማማት ግን እቸገራለሁ፡፡ እንዲያው ለነገሩ እነዚህ ሰማዕታት “ለኢትዮጵያ ሕዝብ ዘላለማዊ የሕዝባዊነት ኃይል መልእክት እያስተላለፉ” የሚኖሩት እንዴት ነው አቦይ? ሦስት ከተሞች (መቀሌ፣ ባህር ዳር እና አዳማ) ላይ የተተከሉ ሀውልቶች “ለኢትዮጵያ ሕዝብ ዘላለማዊ የሕዝባዊነት ኃይል መልእክት የማስተላለፍ ኃይል አላቸው” እያሉን ከሆነ ትንሽ የተጋነነ መሰለኝ፡፡ በኔ እምነት ሰማዕታቱ ዘላለማዊ መልእክት እያስተላለፉ መኖር እንዲችሉ መጀመሪያ ስማቸው (ማንነታቸው) መታወቅ አለበት፡፡ ከዚያም ለሰማእትነት ያበቃቸው ተግባር ምን እንደሆነና መቼና የት እንደተከናወነ በመረጃ ተደግፎ፣ በሰነድነት ተደራጅቶ ለሕዝብ መቅረብ ይኖርበታል፡፡

ይህ ካልሆነ ግን፤ ጊዜ በተቆጠረ፣ ዘመን በተሻገረ ቁጥር እንኳን መላ ሕዝቡ፣ የፖለቲካ አመራሩ ማስታወስ የሚችል አይመስለኝም፡፡ አቶ መለስ የትጥቅ ትግሉ አካል ስለነበሩ የተከፈለውን መስዋእትነት በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ የሚጠቅሱበት ሁኔታ ነበር፡፡ አቶ ኃ/ማሪያም ግን በአንዳንድ ንግግሮቻቸው ማብቂያ ላይ “ዘላለማዊ ክብር ለትግሉ ሰማዕታት” የሚል መፈክር ከማሰማት በዘለለ የሰማእታቱን ስራ ለመጥቀስ የሚችሉበት ሁኔታ ይኖራል የሚል ግምት የለኝም፡፡ ከአቶ ኃ/ማሪያም በኋላ የሚመጣውማ ይህንን ስለማለቱም እርግጠኛ መሆን የሚቻል አይመስለኝም፡፡ በእርግጥ በአስር ሺዎች በሚቆጠሩ ዜጎች፣ ለሁለት አስርት ዓመታት ገደማ የተከናወነን ተግባር መመዝገብ ቀላል ሥራ እንዳልሆነ፤ ሰፊ ጊዜና በርካታ ገንዘብ እንደሚጠይቅ እገምታለሁ፡፡ ይሁን እንጂ፣ ይህንን ታላቅ ተግባር ለማከናወን ጨርቃችንን አንጥፈን በመለመን ገንዘብ ማሰባሰብ ካለብን፣ ያን ማድረግ የግድ ነው፡፡ ሰማእታቱ ውድ ሕይወታቸውን ነው የሰጡት፡፡ እኛ ታሪካቸውን ለመዘገብ ገንዘባችንን፣ እውቀታችንን እና ጊዜአችንን መስዋእት ብናደርግ የሚመጣጠን አይመስለኝም፡፡ በጽሁፌ መግቢያ ላይ እንደጠቀስኩት አቶ ስብሃት ግልጽና ቀጥተኛ ሰው ናቸው፡፡ ያመኑበትን ሃሳብ ለመግለጽ እንደ አንዳንድ የሀገራችን “አድርባይ ፖለቲከኞች” ተለማጭ (ዲፕሎማሲያዊ) ቃላትን አይመርጡም፡፡

ከዚሁ ከአዲስ አድማስ ቃለ ምልልሳቸው ማስረጃ ልጥቀስ፡፡ “… አሁን የሚያሰጋው የመለስን ራዕይ እንደ ቁም ነገር ሳይሆን እንደ መፈክር ይዞ በጥገኝነት ተዘፍቆ የነበረው እንደ መደበቂያ፣ አዲሶች ሊጨማለቁ የፈለጉ ደግሞ እንደ መታወቂያ ይዘው… ችግሮችን እንዳንፈታ፣ እንደ መጋረጃ እንዳይጠቀሙበት ነው…” ይላሉ፡፡ በዚህ ግልጽ አባባላቸው እስማማለሁ፡፡ በመንግስት ይዞታ ስር ያሉ መገናኛ ብዙሃን እንዲህ ያለውን ሁኔታ ጥንቃቄ በተሞላበት ሁኔታ፣ ሕዝቡን በቁጭት ለልማት ሊቀሰቅስ በሚችል መንገድ ቢያቀርቡት መልካም ነው፡፡ ከአቶ ስብሃት ጋር ወደማልስማማበት ሁለተኛ ጉዳይ ላምራ፡፡ ክቡርነታቸው በዚሁ ቃለ ምልልሳቸው ካነሷቸው ጉዳዮች አንዱ የኤርትራና የባህር በር ጉዳይ ነው፡፡ “በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ጊዜ… አስመራ ካልደረስኩ፣ አሰብን ካልያዝኩ” የሚል ኃይል ኢህአዴግ ውስጥ እንደነበር አቶ ስብሃት ከጠቀሱ በኋላ፤ ያ ኃይል አሁን “የተዳከመና ጊዜው ያለፈበት ነው” በማለት ይደመድማሉ፡፡

ቀጥለው ደግሞ፤ “… ይህ መሬት፣ ይህ ዳገት፣ ይህ ወንዝ… የሚባለው በሕዝቦች ወንድማማችነት…” መተካቱንና የሚያቆመውም ኃይል እንደሌለ አስረግጠው ይናገራሉ፡፡ የዚህ ጽሁፍ አቅራቢ ከተቃዋሚ ፓርቲ አመራርነትም፣ አባልነትም፣ ከተለየሁ ሦስት ዓመታት ተቆጠሩ፡፡ እናም፤ በዚህ ወቅት የምደግፈውም የምነቅፈውም የፖለቲካ አቋም የለም፡፡ በባህር በር ጉዳይ ላይ ግን ቀደም ሲል አባልም አመራርም ከነበርኩበት ኢዴፓም ሆነ ከአቶ ስብሃትና ከኢህአዴግ አቋም ጋር አልስማማም፡፡ ከኢዴፓ ጋር የማልስማማው ፓርቲው የባህር በርን በተመለከተ “በሕጋዊ፣ በዲፕሎማሲያዊና በሰላማዊ መንገድ እንዲመለስ አደርጋለሁ” የሚል ድፍን ያለ አቋም ስለሚያራምድ ሲሆን፤ በግሌ የሀገሪቱን ሉአላዊነትና ለዘመናት የቆየ ዳር ድንበር ማስከበር የሚቻለው በሰላማዊና በዲፕሎማሲ መንገድ ብቻ ሳይሆን አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ በጦርነት ጭምር መሆን አለበት የሚል አቋም አለኝ፡፡ ፈረንጆቹ “War is an extension of diplomacy” ይላሉ፡፡ እናም ኢዴፓ “ዲፕሎማሲያዊና ሰላማዊ” ጥረት አደርጋለሁ ብላ ማቆሟ ትክክል አይመስለኝም፡፡ የዲፕሎማሲው ቀጣይ ትግል ምን እንደሚሆን በግልጽ ማስቀመጥ ያለባት ይመስለኛል፡፡ “ኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤት መሆን አያስፈልጋትም፡፡ ካስፈለገ እንከራያለን” በሚለው የኢህአዴግ አቋም አልስማማም፡፡ ከዚህ በስተቀር በሌሎቹ የኢህአዴግ መሰረታዊ (Pillar) አቋሞች ዙሪያ ልዩነት እንድፈጥር ግድ የሚለኝ ነገር በዚህ ወቅት የለም፡፡ አቶ ስብሃት እና ፓርቲያቸው ኢህአዴግ የኢትዮጵያን የባህር በር “ባለቤትነት” ጉዳይ አሳንሰው ማየታቸውና ጭራሽ እንደ አልባሌ ሸቀጥ መቁጠራቸው ምንጊዜም ይገርመኛል፡፡

እነርሱ ይህንን አቋም ከያዙ እነሆ አርባ ዓመት ሊሆናቸው ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ሁለት ትውልድ ማለት ነው፡፡ አቶ ስብሃት እንደሚያስቡት የባህር በር ጉዳይ “በሕዝቦች ወንድማማችነት” የሚተካ ቢሆን ኖሮ አጀንዳው አጀንዳ ሆኖ ሁለት ትውልድ ድረስ አይዘልቅም ነበር፡፡ እንዲያውም ሀገሪቱ በኢኮኖሚ እያደገች ስትመጣ በዚያው ልክ የቅርብም የሩቅም ምቀኛና ጠላት ማሰፍሰፉ አይቀርም፡፡ የችግሩም መጠን እየጨመረ ሲመጣ የባህር በር አስፈላጊነት እየጨመረ እንደሚመጣ ይታየኛል፡፡ ክቡር አቶ ስብሃት! በዚህ ወቅት የባህር በር ጉዳይ “በሕዝቦች ወንድማማችነት ተተክቷል፡፡ የህዝብ አጀንዳ አይደለም” ብለው የሚያምኑ ከሆነ አንድ ነገር ይፍቀዱልኝ፡፡ ሩቅ ሳልሄድ የህወሐት እትብት በተቀበረበት በትግራይ ክልል ያለው ሕዝብ በዚህ ጉዳይ ላይ ያለውን አቋም በተመለከተ ፊርማ ላሰባስብ፡፡ አንዳንድ “ሸረኞች” እንዳይተናኮሉኝ ክቡርነትዎ በመንግስትም በፓርቲም መዋቅር ባለዎት ግንኙነት ለሚመለከታቸው ሁሉ ይንገሩልኝ፡፡ ለፖሊስም ለደህንነትም ይንገሩልኝ፡፡ ፊርማውን ለማሰባሰብ ስፖንሰርም፣ ረዳትም፣ ድርጅትም አያስፈልገኝም፡፡ እኔ ራሴ እበቃለሁ፡፡ መላ ትግራይን በእግሬም፣ በመኪናም፣ በፈረስም ዞሬ ፊርማውን አሰባስቤ ውጤቱን ለክቡርነትዎ ላቅርብ፡፡

ከዚያ በኋላ “ይህ መሬት፣ ይህ ዳገት፣ ይህ ወንዝ… የሚባለው በሕዝቦች ወንድማማችነት ተተክቷል” የሚለው የእርስዎ “Hypothesis” (ንድፈ-ሃሳብ) ስህተት ወይም እውነት መሆኑን ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ይህንን ለርስዎ ልተወውና በዚሁ በጉዳይ ላይ ሌላ የመከራከሪያ ነጥብ ላንሳ፡፡ በኢህአዴግ በኩል ሌላው ተደጋግሞ የሚነሳው የመከራከሪያ ሃሳብ “ለባህር በር ተብሎ ጦርነት ውስጥ መገባት የለበትም፡፡ ነፍስ መጥፋት የለበትም፡፡ ከማንም በላይ እኛ የጦርነትን አስከፊነት እናውቃለን፡፡ ሕይወት ይቀጥፋል፣ ንብረት ያወድማል፣ ልማት ያደናቅፋል፡፡ ስለዚህ መዋጋት የለብንም፡፡ ወደብ እንደማንኛውም አገልግሎት እንከራያለን…” የሚል መንፈስ አለው፡፡ በበኩሌ የጦርነትን አስከፊነት እገነዘባለሁ፡፡ አውዳሚነቱንም አውቃለሁ፡፡ ይሁን እንጂ፣ ጦርነት አስከፊ ነው ብለን ስላወገዝነው፣ ስለሸሸነው ወይም እኛ ሰላማዊ ስለሆንን አይቀርልንም፡፡ ጦርነት በአንድ ወገን ውሳኔ የሚቆም ጉዳይ አደለም፡፡ ያ ቢሆን ኖሮ ባድመና ሽራሮ ላይ፣ ፆረናና ዓይጋ ተራራ አናት ላይ፣ ዛላንበሳና ቡሬ ግንባር ላይ፣… ባልተዋጋን ነበር፡፡ በትጥቅ ትግሉ ወቅት በየጥሻው ለወደቁ ወገኖቻችን ሀዘን የተከልነውን ድንኳን ሳንነቅል ተጨማሪ ስልሳ እና ሰባ ሺህ ዜጎችን ባልቀበርን ነበር፡፡ ስለሆነም፣ ጦርነት የምርጫ ጉዳይ ስላልሆነ መጥላትም መፍራትም አይገባንም፡፡ በጦርነት የሚጠፋው ሕይወታችን እና የሚወድመው ሀብት ንብረታችን ብቻ ቁምነገር ተደርጎ መወሰድ የለበትም የሚል እምነት አለኝ፡፡ ይልቁንም፣ ቁም ነገር መሆን ያለበት ሕይወት የገበርንለት እና ሀብት ያወደምንለት ጦርነት ዓላማና ግብ ይመስለኛል፡፡ በዚህ ረገድ ከኤርትራ ጋር ያደረግነው ጦርነት ዓላማና ግብ ምን እንደሆነ እስከ አሁን አልገባኝም፡፡

እውነት ዓላማችን ምን ነበር? ሰላም? መሬት? ድንበር?... እና ይሄ ዓላማ ተሳክቶ የምንፈልገውን ሰላም አግኝተናል? ዳር ድንበራችንን በቅጡ አስከብረን በድንበር አካባቢ የሚኖሩ ዜጎች የተረጋጋ ሕይወት እየኖሩ ነው?... ከሆነ እሰየው ነው፡፡ ግን አይመስለኝም! እኔ እስከማውቀው ድረስ በአስር ሺዎች ሕይወት የገበርንበት ጦርነት ውጤት አመድ አፋሽ ያደረገንን የአልጀርስ ስምምነት እና “ባለ አምስት ነጥብ የሰላም ስምምነት” የተሰኘ የኩነኔ ሰነድ ይመስለኛል፡፡ ይሄ ታዲያ ከተከፈለው ዋጋ ጋር ተመጣጣኝ ነው? ይህንን ለማግኘት መዋጋትስ ነበረብን? አይመስለኝም! ለዚህም ነው ኢህአዴግ ውስጥ “በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ጊዜ… አስመራ ካልደረስኩ፣ አሰብን ካልያዝኩ” ይል የነበረው ኃይል “ትክክል አልነበረም” ብሎ ለመደምደም የሚያስቸግረው፡፡ ክቡር አቶ ስብሃት፣ ተወልጄ ባደግኩባት በቀድሞዋ የጁ አውራጃ በልጅነቴ ያካባቢዬ እረኞች ያቀነቅኗት የነበረች አንዲት ግጥም እስከ አሁን ድረስ ጆሮዬ ላይ ታቃጭላለች፡፡ ግጥሟ “እንኳን ለሴት እና ለቁም ነገሪቱ፤ በዱባ ተጣልተው ሁለት ጃርቶች ሞቱ” የምትል ናት፡፡ ይህቺን በውስጧ ትምክህት ያዘለች ባልቴት ግጥም የጠቀስኩት አለምክንያንት አይደለም፡፡ ከዚሁ ጋር ተያያዥነት ያለው ሃሳብ በንጽጽር ለማቅረብ አስቤ ነው፡፡

ከላይ ለማመልከት እንደሞከርኩት ለግብ የለሽ ዓላማ ሕይወታችንን መገበር ያልሳሳነው እኛ ኢትዮጵያውያን፣ የሀገራችን አንጡራ ሀብት ለሆነው የባህር በር መስዋእትነት ብንከፍል ምን ይለናል? ለማለት ፈልጌ ነው፡፡ አዎ! ምንም አይለንም! እንዲህ ያለውን ተግባር ያደጉና የሰለጠኑ ሀገሮች ሕዝቦች ጭምር (ለምሣሌ፤ እንግሊዞች በብዙ ሺህ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ለሚገኙት የፎክላንድ ደሴቶች) የፈጸሙት በመሆኑ ትዝብት ላይ የሚጥለን፣ ከዓለም መድረክ ላይ የሚያገለን አይሆንም፡፡ ለዓመታት እንደታዘብኩት፣ እንደ ድርጅት የኢህአዴግ አንዱ ችግር በአንድ ወቅት በአንድ ጉዳይ ላይ አንድ የሆነ አቋም ከያዘ እዚያው ላይ ክችች ማለቱ ነው፡፡ ኢህአዴጎች አንዴ አቋም ከያዛችሁ በጊዜ ሂደት አቋም መቀየር የሚቻል አይመስላችሁም ልበል? ፖለቲካ ግን እንደዚያ ተቸካይ (Static) አይደለም፡፡ ፖለቲካ ሰዎች የሚያከናውኑት ተግባር በመሆኑ ምንጊዜም በለውጥ ሂደት ውስጥ (Dynamic) ነው፡፡ እናም፤ በቃለ ምልልስዎ እንደገለጡት “የሕወሓት ፕሮግራም ብቁና የማይለወጥ ነው” የሚለውን ፖለቲካን ቀኖና ያደረገ፣ ፍንክች የማይል (Rigid) አቋም ብትፈትሹት መልካም ነው፡፡ ለሀገርና ለሕዝብ ጥቅም ስትሉ መለወጥ ያለበትን ለውጡ፡፡ መሻሻል ያለበትን አሻሽሉ፡፡

(ለነገሩ ጊዜና ትውልድ ማሻሻላቸው እንደሆነ አይቀሬ ነው) ኢህአዴግ የመላእክት ስብስብ አይደለም፡፡ ሰዎች ደግሞ ትክክልም ስህተትም ይሰራሉ፡፡ በዚህ ረገድ ኢህአዴግ ከሰራቸው ስህተቶች አንዱ የባህር በርን አስመልክቶ የያዘው አቋም ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ “የኤርትራ ሕዝብ የራሱን ዕድል በራስ የመወሰን እስከ መገንጠል መብት አለው” የሚለውን የኢህአዴግ አቋም አሁን ላይ ሆኜ ሳስበው ስህተት አደለም፡፡ ስህተቱ የኤርትራ ሕዝብ የራሱን እድል በራሱ በሚወስንበት ወቅት እግረ መንገዱን የሚጨፈልቃቸው የኢትዮጵያ ሕዝቦች መብትና ጥቅሞች አሉ? ካሉ ምን ምን ናቸው? መፍትሄውስ ምንድነው? ብሎ በጥልቀትና በስፋት መክሮ የሕዝቡንም ስነ ልቡና አገናዝቦ አቋም አለመያዙ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ በዚህ መልኩ ታስቦበት ቢሆን ኖሮ፣ ኤርትራውያን ነፃነታቸውን ሲያገኙ ኢትዮጵያውያንም አንጡራ ሀብታቸው የነበረውን የባህር በራቸውን አያጡም ነበር፡፡ በዚህ መልኩ ታስቦበት ቢሆን ኖሮ፣ የኤርትራ ነፃነት በኢትዮጵያ ኪሣራ (With the expense of Ethiopia) እውን አይሆንም ነበር፡፡ እናም፤ እንዲያው በደፈናው “ሕወሓት… በይሉኝታ ምክንያት ድክመትን ደብቆ አድበስብሶ ማለፍ ባህሉ አደለም” ከምትሉን በተጨባጭ አረጋግጡልን፡፡

ክቡር ሆይ! በዚያ ወቅት እናንተ (ኢህአዴግ) ያን አቋም የያዛችሁት ቅን አሳቢ ጭንቅላታችሁ ያመነጨውን ጨዋ ፍልስፍና ወይም ንድፈ ሃሳብ መነሻ አድርጋችሁ እንደሆነ አስባለሁ፡፡ ከአንዳንድ የኢህአዴግ ሰነዶችና ከአመራሩ ቃለ ምልልሶች እንደተረዳሁት፣ የእናንተ ንድፈ ሃሳብ “በኢትዮጵያም ሆነ በኤርትራ ሰላም ከሰፈነ፣ ሕዝብ ከጦርነት ወጥቶ ልማት ላይ ካተኮረ፣ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱን ድንበር አይከላውም፡፡ እነሱ ገበያ ይፈልጋሉ፡፡ እኛ የባህር በር ያስፈልገናል፡፡ እናም ሁላችንም የምንፈልገውን እናገኛለን…” የሚል እንደሆነ እገምታለሁ፡፡ እንዲህ ብሎ ማሰብ ክፋት የለውም፡፡ ይሁንና በፖለቲካ ውስጥ የዋህነት አጉል ጨዋታ ነው፡፡ ፖለቲከኛ እንደ ቼዝ ተጫዋች መሆን አለበት፡፡ ራሱ የሚያንቀሳቅሰውን ብቻ ሳይሆን ተቃራኒው ወገን የሚጫወተውን ጭምር በጥንቃቄ ማጤን ይጠበቅበታል፡፡ ኢህአዴግ ይህንን ባለማድረጉ “ዘይዋዓልኩሉ ዘረባ…” የሚል ስንኝ ደርድረን፣ ዜማ አውጥተን በትካዜ እያቀነቀንን እንደ ሀገርና እንደ ሕዝብ ሁላችንም ዋጋ ከፍለንበታል፡፡ እዚህ ላይ “ታዲያ ምን አድርጉ ነው የምትለው? እንዋጋ ነው? ሰላማዊ ሰልፍ ነው? እንዝመት ነው...” የሚል ጥያቄ ይነሳ ይሆናል፡፡ በኔ እምነት ጦርነት የምርጫ ጉዳይ አይደለም፡፡

አስፈላጊ ከሆነ (war of necessity) አይቀርልንም፡፡ እናም ጦርነትን ማስፈራሪያ ባናደርገው ሸጋ ነው፡፡ ለነገሩ ኢህአዴግ የሚያወግዘው የሌሎችን የጦርነት ፍላጎት እንጂ ራሱ ያመነበትን ጦርነትማ ‘ነፍስ ይጠፋል፣ ንብረት ይወድማል፣ ሰው ይሞታል፣ ልማት ይቆማል፣…’ ብሎ እጁን አጣጥፎ አልተቀመጠም፡፡ በሰሜንም በምስራቅም ሲዘምት አይተናል፡፡ ክቡር ሆይ! ይህንን ሁሉ ሀተታ ላይ ታች እያጣቀስኩ ያቀረብኩት እም ዐልቦ ምክንያት አደለም፡፡ በፖለቲካ ምንም ዓይነት “ተዘጋ” የሚባል አጀንዳ የለም፡፡ አንድም ሰው ቢሆን አምኖ መስዋእትነት ሊከፍልበት እስከተዘጋጀ ድረስ ተንቆና ተንቋሾ የትም የሚጣል የፖለቲካ አጀንዳ ሊኖር አይችልም፡፡ በዓለም ላይ በአንድ ሰው የተጀመሩ በርካታ አጀንዳዎች በጊዜ ሂደት ሚሊዮን ተከታዮችን ያፈሩበት ሁኔታም ተስተውሏል፡፡ እናም የባህር በርን ጉዳይ ከመጠን ባለፈ መልኩ ማናናቁ ጠቃሚ መስሎ አይታየኝም፡፡

ይህ ጉዳይ የሕዝብ አጀንዳ መሆንና አለመሆኑን ለማወቅ መድረክ ከፍተን በቅን ልቡና እንወያይ፣ እንከራከር፡፡ የውይይቱና የክርክሩ መደምደሚያ ወደ ቀጣዩ እርምጃ ይመራናል፡፡ ከዚህ ውጪ ግን ማዶ ለማዶ ሆኖ ቃላት መወራወሩና አንዱ የሌላውን ሃሳብ እያጣጣለ “ትክክለኛው የእኔ መንገድ ብቻ ነው” ብሎ መታበይ የዴሞክራሲ መንገድ አይመስለኝም፡፡ እንዲህ ያለው አካሄድ የአናሳውን የመደመጥ መብት ያንቃል፣ ይጨፈልቃል፡፡ ለመብትና ለጥቅሙ ቆመንለታል ለምንለው ሕዝብም ሆነ እንወዳታለን ለምንላት ሀገራችንም አይበጃትም፡፡

  1. 1ኛ) ምንም ልለውጣቸው የማልችላቸውን ነገሮች እንድቀበል፣ አደብ እንድገዛ እንዲያደርገኝ
  2. 2ኛ) ልለውጣቸው የምችላቸውን ነገሮች እንድለውጣቸው ድፍረቱን እንዲሰጠኝ
  3. 3ኛ) በ1ኛውና በ2ኛው መካከል ያለውን ልዩነት አውቅ ዘንድ ዕውቀት እንዲሰጠኝ! የፋሲካ ስጦታ

ጀርመናዊው ባለቅኔ ሺለር ስለዳሞንና ፒንቲያስ (የሊቁ የፓይታጐረስ ተማሪዎች ናቸው) ወዳጅነት የሚከተለውን ይለናል፡፡ እንደተረት ብንወስደው ለዛሬ ቀን ይሆነናል፡፡ ዲዮኒሶስ ለተባለው መስፍን፤ ካራ የያዘ ዳሞን የሚባል ወንጀለኛ ይዘናል ብለው ባለሟሎቹ ወደ ችሎቱ አቀረቡለት፡፡ መስፍኑም በግዛቴ ላይ አምፀሃል በሚል ሞት እንደሚገባው ገለፀለት፡፡ “ሞትን አልፈራም” አለው ዳሞን፡፡ “ሆኖም መሥፍን ሆይ! የሦስት ቀን ጊዜ ብትሰጠኝ ምህረት እንደሰጠኸኝ እቆጥረዋለሁ” አለው፡፡ “የሦስት ቀን ጊዜ ለምን ፈለግህ?” አለ መስፍኑ፡፡ “እህቴን ድሬ ለመመለስ ነው፡፡ እኔ ከቀረሁኝ የሚዋሰኝ ጓደኛ በመያዣነት አንተ ዘንድ በዋስነት እንዲቀመጥ አደርጋለሁ” ሲል ተናገረ፡፡ መሥፍኑም፤ “ሦስት ቀን ሸልሜሃለሁ፡፡ ከዚያ ያለፍክ እንደሆነ ግን፣ ጓደኛህ በመስቀል ላይ ይሰቀላል” አለው፡፡ ጓደኛውን ጠርቶ ይህንኑ ነገረው፡፡ ጓደኛውም ዋስ ለመሆን ፈቃደኛ መሆኑን ገለፀ፡፡ ዳሞን እህቱ ያለችበት ቦታ ሄዶ፤ ድል ያለ ሠርግ ደገሰ፡፡

ሠርጉን አሳክቶ ጉዞ ወደ አገሩና ዋስ ወደሆነው ወዳጁ መልስ አደረገ፡፡ እየተጥደፈደፈም መንገድ ቀጠለ፡፡ መንገድ ላይ ዶፍ ዝናብ ጣለና ወንዝ ሞላ፡፡ ወንዙ እስኪጐድል ይጠብቅ ጀመረ፡፡ በጅረቱ ዳር ተንከራተተ፡፡ ወንዙ ግን አልጐደለም፡፡ ታንኳም አልመጣ አለ፡፡ “ጀንበር ከጠለቀች ወዳጄ መሞቱ ነው” ሲል አሰበ፡፡ በወንዙ ዳር ተንበርክኮ ፀለየ፡፡ የውሃው መጠን መብዛቱ በቀጠለ ጊዜ፤ ካበደው ጅረት ውስጥ ዘሎ ገባ፡፡ ውሃው፤ በአምላክ ፈቃድ፣ ወደ ዳርቻው ጣለው፡፡ አምላኩን አመስግኖ ሩጫውን በከተማው አቅጣጫ ቀጠለ፡፡ ጥቂት እንደሄደ ግን ቀማኛና ሽፍቶች ብቅ አሉበት፡፡ ካራቸውን መዘው አስፈራሩት፡፡ “ንብረት የለኝም፡፡ ያለኝ ንብረት ነብሴ ብቻ ናት፡፡ ነብሴን ደግሞ ለንጉሡ መስጠት አለብኝ!” ቢልም ንቅንቅ አልል አሉት፡፡ ስለዚህ በፍጥነት ያንደኛውን ካራ ነጥቆ አንድ ሶስቱን ሲጥላቸው፤ የቀሩት እግሬ አውጪኝ አሉ፡፡ ውሃ ጥሙንና በረሃውን ተቋቁሞ እየበረረ እንደምንም አገሩ ደረሰ፡፡

ዘበኛውን አገኘው፡፡ እሱም “በከንቱ አትልፋ፡፡ ወዳጅህን ለማዳን አትችልም፡፡ ይልቅ የራስህን ነብስ አድን” አለው፡፡ “ግዴለም የጣርኩትን ያህል ጥሬ ልደርስለት እሞክራለሁ፡፡ ካልሆነም በምድር ፍቅርና ዕምነትን አስተምሬ፤ በሰማይ ቤት አገኘዋለሁ” ብሎ ወደከተማው ማህል ዘለቀ፡፡ ህዝቡ የስቅላቱን የመስቀል እንጨት፣ ከቦ ቆማል፡፡ ወዳጁን በገመድ ሲስቡት አየ፡፡ “እኔን ስቀሉኝ! ለወዳጄ ደርሼለታለሁ!” አለ፡፡ ህዝቡ ጉድ አለ ጓደኛሞቹ ከስቅላቱ እንጨት ሥር ተቃቀፉና መላቀስ ጀመሩ፡፡ ሰው ሁሉ አብሮዋቸው አለቀሰ፡፡ መሥፍኑ ይሄን ተዓምር ሰምቶ ሰብዓዊ ርህራሄ ተሰማው፡፡ ወደዙፋኑ አስጠራቸውና፤ “የፈለጋችሁት ይሄው ሆነላችሁ ሌላ ነገር ሳይሆን ልቤን ማረካችሁ፡፡ ልመናዬን ስሙኝ እባካችሁን በማህበራችሁ ሶስተኛ ልሁን” ሲል ተቀላቀላቸው፡፡

                                                          * * *

ለጓደኛ ሲሉ መሥዋዕት መሆን ታላቅ ነገር ነው! ዕውነተኛ ፍቅር የሚመጣውና የሚረጋገጠውም ለሌሎች ለማለፍ ዝግጁ ከመሆን ነው፡፡ ያለንን ፍቅር በመስጠት የሌሎችን ልብ መርታት የድሎች ሁሉ ድል ነው! ፋሲካን በዚህ መንፈስ ማክበር ታላቅ ፀጋ ነው!! በዓሉ የሁላችንም እንዲሆን የታረዘ ይልበስ፡፡ የታሰረ ይፈታ፡፡ የነገደ ይቅናው፡፡ የተማረ ይወቅ፡፡ የቦለተከ የህዝብ ዳኝነት ያግኝ፡፡ የተሰሩ መንገዶች ቀና መራመጃ ይሁኑ፡፡ “ፈጣን ነው ባቡሩ” ያልነው ተሳፋሪዎችን ጥሎ አይብረር፡፡ “ያልተመለሰው ባቡር” አዲሱን ባቡር አይማ! ፋሲካው፤ ስቅለትን፣ እሾህ - አክሊልን፣ ግርፋትን፣ ህመምን ያሳየንን ያህል፤ ትንሣዔን እርገትን፤ ለሌሎች ስንል መስዋዕት መክፈልን ያስተምረን ዘንድ፤ ሀገራችንን ህዝባችንን እንድናስብ ልቡናውን ይስጠን፡፡ የኑሮ ውድነትን ለዓመታት ያየነው መሆኑን አንዘነጋም፡፡ የዛሬ ገበያ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ፤ የተጠራቀመ መሆኑንም ልብ ማለት ያባት ነው፡፡ ሆኖም የባሰ አታምጣን እንፀልይ! በዓሉን በደስታና በፌሽታ ለማክበር ያለን ጓዳ - ጐድጓዳ ቆፍሮ፣ የመሶብን ተቃምሶ፣ “ከዓመት ዓመት አድርሰን” ማለት ለባዩም ለሚባለውም አንዳች የሁለትዮሽ ፀጋ እንደሚያጐናጽፍ አይታበልም፡፡

ይሄንን በባዶ አንጀት የማለት አቅም ላጣው ማዘን፣ መባባት ተገቢ ነው፡፡ በሀሰት መስክረው እንዲሰቀል ያደረጉትም ሆነ፤ ከደሙ ንፁህ ነኝ” ያለውም፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ አሳልፎ የሰጠውን፣ የይሁዳን ድርጊት የፈፀመና፤ በሰው ልጆች ላይ ግፍና በደል ይፈፀም ዘንድ ድንጋይ ያቀበለ የእጁን ይስጠው፡፡ ድንጋይ የመረጠም ሁሉ፤ የእጁን አይጣ! ዓይነተኛ መማሪያ ሆኖ፤ ልንጠበብ፣ ልንጠነቀቅና መንፈሳዊ ትንሣዔን ልናገኝ ይገባል፡፡ በዓሉ የፌሽታና የደስታ የሚሆንልን ልባችን ንፁህ ሲሆን ነው፡፡ ልባችን ንፁህ የሚሆነው እጃችን ንፁህ ሲሆን፣ አዕምሮአችን ከግፍ የፀዳ ሲሆን፣ ቃል የገባነውን ለመፈፀም ነፃ አስተሳሰብ ሲኖረን፣ ኃጢያትን ፈርተን ሳይሆን ዲሞክራሲ እንዲዋሃደን ስንወድ፣ ፍትህ ለሰው ልጅ እኩልነት መገለጫ፣ የሌሎች ደስታ ደስታዬ ነው መባያ እንዲሆን ማድረግ ማለት ነው፡፡ ስንበላ የማይበሉትን እናስባቸው፡፡ ስንናገር የማይናገሩትን እናስባቸው፡፡ ስናሸንፍ የተሸነፉትን እናስባቸው፡፡ ስንገዛ የተገዢዎቹን መብትና ነግ በእኔን እናስብ፡፡ ስለትንሣዔ ስናስብ ስለኢትዮጵያ ትንሣኤም በስፋት እናስብ!! መልካም ትንሣዔ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ!!

Published in ርዕሰ አንቀፅ
Page 12 of 14