“ህገ መንግስታዊ መብታችንን በቀላጤ ተቀምተናል” ተማሪዎቹ ባለፈው ዓመት የ6 አመት የርቀት የህግ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ የአዲስ አበባ ማዕከል ተመራቂ ተማሪዎች፣ “የህግ መውጫ ፈተና” ካልተፈተናችሁ ድግሪያችሁን ማግኘት አትችሉም መባላቸውን በመወቃወም ከዩኒቨርስቲው ጋር እየተሟገቱ ነው፡፡ ዩኒቨርሲቲው በበኩሉ፤ ከትምህርት ሚኒስቴር የወረደልኝን መመሪያ ነው ተግባራዊ ያደረግሁት ብሏል፡፡ 135 የሚሆኑ ተማሪዎች በፊርማቸው አስደግፈው በተወካዮቻቸው አማካይነት ለዝግጅት ክፍላችን ባቀረቡት መረጃ፤ ለ6 አመት የህግ ትምህርታቸውን በLLB ደረጃ በርቀት ሲከታተሉ ቆይተው ካጠናቀቁ በኋላ በትምህርት ውላቸው ላይ የሌለውን “የህግ መውጫ ፈተና” መውሰድ አለባችሁ እንደተባሉና ካልሆነ ድግሪያቸው እንደማይሰጣቸው ከዩኒቨርሲቲው እንደተገለፀላቸው ጠቁመዋል፡፡ “ትምህርት ሚኒስቴር ያወጣው መመሪያ ነው” በሚል እያንዳንዳቸው 674 ብር እስከ የካቲት 30 ቀን 2007 ዓ.ም በመክፈል ፈተናውን እንዲወስዱ ሰሌዳ ላይ በተለጠፈ ማስታወቂያ እንደተገለፀላቸው የጠቆሙት ተማሪዎቹ፤ “ይሄ ቀድሞ የማናውቀው መመሪያ፤በህገ መንግስቱ የተሠጠንን መብት የሚያሣጣን ነው” ሲሉ ተቃውመዋል፡፡ የተመራቂዎቹ ተወካይ አቶ ሙሉጌታ ጉግሣ ለአዲስ አድማስ እንደገለፀው፤ ተመራቂዎች ፈተናውን ይውሰዱ ቢባልና አንድ ተማሪ በፈተናው ቢወድቅ የ6 አመት ልፋቱን ዋጋ ቢስ የሚያደርግ በመሆኑ አመክንዮአዊ አይሆንም ብሏል፡፡ ፈተናውን ለመውሰድ 674 ብር ክፈሉ መባሉም ዩኒቨርስቲው ያለ አግባብ የገንዘብ መሰብሰብ ሥራ ውስጥ የገባ ያስመስለዋል ሲል ተወካዩ አክሎ ገልጿል፡፡ የተማርንበትን የምስክር ወረቀት የማግኘት ህገ መንግስታዊ መብት አለን ያለው አቶ ሙሉጌታ፤ “አሁን ግን ህገመንግስታዊ መብታችንን በአንዲት ደብዳቤ (ቀላጤ) እንደተቀማን እየተነገረን ነው” ብለዋል፡፡ የለፋንበትን ያለቅድመ ሁኔታ የማግኘት መብት በደብዳቤ መቀማት የሚያስችል የህግ ድንጋጌ የለም፤ ቢኖርም ህገ መንግስቱን የሚቃረን ነው ያለው የተማሪዎቹ ተወካይ፤ “በተደጋጋሚ በበላይ አመራሮች በፖሊሲ ደረጃ የተተገበረ አሠራር ነው” የሚል ምላሽ እንደሚሰጣቸው ጠቁመው፤ ፖሊሲው ግን ምን እንደሆነ በግልጽ አይታወቅም ብለዋል፡፡ “ይህ የህግ መውጫ ፈተና ፖሊሲ ነው ካሉ ለምን በሚገባ አያረጋግጡልንም” ያሉት ተመራቂዎቹ፤ ሌሎች ዩኒቨርስቲዎች በተመሳሳይ በLLB ለሚያስመርቋቸው የርቀት ተማሪዎች ያለ መውጫ ፈተና ሠርተፊኬታቸውን እየሰጡ መሆኑን በተጨባጭ እናውቃለን፤ ማስረጃም አለን ብለዋል፡፡ “የኛ ከሌላው የሚለየው በምንድን ነው?” ሲሉም ጠይቀዋል፡፡ “የህግ መውጫ ፈተና መኖሩን ፈጽሞ አንቃወምም” የሚሉት ተመራቂዎቹ፤ ነገር ግን ፈተናው መዘጋጀትና መሰጠት ያለበት በፍትህ አካላት ነው ሲሉም ሞግተዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ ምላሽ እንዲሰጡን በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ የርቀት ትምህርት ማስተባበሪያ የፈተና ክፍል ተጠሪ አቶ በለጠ ተክሌን አነጋግረን በሰጡን ምላሽ፤ መመሪያውን መንግስት እንዳወጣውና በባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ብቻ ሳይሆን በሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን የገለፁ ሲሆን ዩኒቨርሲቲው ከመንግሥት መመሪያ ውጪ ሊሆን እንደማይችልም ተናግረዋል፡
Published in ዜና

በድሬደዋ ከተማ ጋብቻ በፈፀሙ በሁለተኛው ወር ሚስቱን በእለታዊ ግጭት ተነሳስቶ በአሰቃቂ ሁኔታ በዱላና በድንጋይ ደብድቦ የገደለው ግለሰብ የእድሜ ልክ ጽኑ እስራት ተፈረደበት፡፡
ረመዳን ዳዊ አህመድ የተባለው የ40 አመት ጐልማሣ፤ የካቲት 15 ቀን 2007 ዓ.ም ወንጀሉን ከፈፀመ በኋላ ከአካባቢው በመሠወር አለማያ ከተማ አጐቱ ጋ ተደብቆ እንደነበር የገለፀው ፖሊስ፤ በክትትል ግለሰቡ ተይዞ ምርመራ  ከተደረገበት በኋላ ክስ የተመሰረተበት ሲሆን ፍ/ቤቱ የቀረበለትን ማስረጃ መርምሮ ግለሰቡን በእድሜ ልክ ጽኑ እስራት እንዲቀጣ ወስኗል፡፡
የድሬደዋ ፖሊስ ኮሚሽን የህዝብ ግንኙነት ዲቪዢን ሃላፊ ዋና ኢንስፔክተር ገመቹ ካቻ፤ ግለሰቡ ከዚህ ቀደም በሰው አካል ላይ ጉዳት በማድረስና ወንጀለኛን በማስመለጥ የወንጀል ድርጊቶች በፍ/ቤት ቅጣት ተወስኖበት የእስር ጊዜውን ጨርሶ ከማረሚያ ቤት የወጣ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
የሟች በአሠቃቂ ሁኔታ መገደልን ተከትሎ የድሬደዋ ነዋሪዎች ሠላማዊ ሠልፍ በማድረግ ወንጀለኛው ተመጣጣኝ ፍርድ እንዲሰጠው መጠየቃቸውን ያስታወሱት ኢንስፔክተር ገመቹ፤ ህብረተሰቡ ወንጀለኛው ከተደበቀበት እንዲያዝ በመጠቆምና መረጃ በመስጠት  ከፍተኛ ትብብር ማድረጉን በመጠቆም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
በ20ዎቹ የዕድሜ ክልል ላይ የነበረችው ሟች ከትዳር በፊት ከሌላ የወለደችው የአንድ ልጅ እናት ነበረች ተብሏል፡፡

Published in ዜና

የአፍሪካ ሀገራትን አጠቃላይ እንቅስቃሴና ተጨባጭ እውነታ በጥናት እየፈተሸ ደረጃ በመስጠት የሚታወቀው “አፍሪካ ክራድል” ድረገፅ፤ ሰሞኑን 10 ተፅዕኖ ፈጣሪ የአፍሪካ አገራትን ይፋ ያደረገ ሲሆን ኢትዮጵያ ከደቡብ አፍሪካ በመቀጠል ሁለተኛዋ ተፅዕኖ ፈጣሪ አገር ተብላለች፡፡ የሀገራቱ የተፅዕኖ ፈጣሪነት ደረጃ የተሠጠው በጦር ሃይል፣ በዲፕሎማሲ እና በአለማቀፍ ደረጃ ባላቸው እውቅና ሲሆን የመጀመሪያ ደረጃ የተሠጣት ደቡብ አፍሪካ በአህጉሪቱ ብቸኛ የ “ቡድን 20 እና የ “BRICS” አባል ሀገር እንዲሁም የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት ቀዳሚ የንግድ ሸሪክ መሆኗ ለደረጃው አብቅቷታል ተብሏል፡፡
የደቡብ አፍሪካ ስም ሲነሳ የማንዴላ የአፓርታይድ ተጋድሎ አብሮ እንደሚነሣ የጠቆመው ሪፖርቱ፤ ዛሬ በሀገሪቱ ለተገነባው ዲሞክራሲያዊ ስርአት የማንዴላና ተከታዮቻቸው የእነታቦ ኢምቤኪ አስተዋጽኦ የጐላ እንደሆነ ጠቁሟል፡፡
በተፅዕኖ ፈጣሪነት ሁለተኛ ደረጃ የተሠጣት ኢትዮጵያ፤ በመፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስሟ 44 ጊዜ ያህል መጠቀሱን፣ በታሪክ፣ ቅኝ ባለመገዛት፣ በጦር ሃይል፣ በፖለቲካና ዲፕሎማሲ ወደር የለሽ ታሪክና ተሞክሮ እንዳላት በማውሳት በዚህ ረገድ ከአፍሪካ አገራት የሚስተካከላት እንደሌለ ሪፖርቱ ጠቁሟል። አገሪቱ በአድዋ ጦርነት የተቀዳጀችውን ድል ተከትሎ ከ20 በላይ የሚሆኑ የአፍሪካ ሀገራት የኢትዮጵያን የባንዲራ ቀለማት በተለያየ ቅርፅና ይዘት ለመጠቀም እንደተገደዱ፣ የቡና የትውልድ አገር እንዲሁም፣ የሰው ዘር መገኛ መሆኗን፣ የራሷ የቀን አቆጣጠርና ፊደላት እንዳላትም የጠቆመው ሪፖርቱ፤ ነዳጅ ሳይኖራት ከድህነት ለመውጣት የምታደርገው ጥረት ኢኮኖሚዋን በከፍተኛ መጠን እያሳደገው መሆኑን፣ በጦር ሃይልም ቢሆን ጠንካራ ሃይል ከገነቡ የአፍሪካ ሀገሮች ተጠቃሽ እንደሆነች አመልክቷል፡፡
ሀገሪቱ ለወደፊቱ በአለም ላይ ተፅዕኖ ይፈጥራሉ ተብለው ተስፋ ከሚጣልባቸው የአፍሪካ ሀገራት አንዷ እንደምትሆንም ሪፖርቱ ተንብይዋል።
ከኢትዮጵያ ቀጥሎ ግብፅ በ3ኛ ደረጃ ተፅዕኖ ፈጣሪ ተብላለች፡፡ በርካታ የተማሩ ሰዎች አሏት የተባለችው ኬንያ 4ኛ ደረጃ ሲሰጣት፣ የአለማቀፍ ኩባንያዎች መቀመጫ የተባለችው ሞሮኮ 5ኛ፣ ቀዳሚ የኢኮኖሚና የሃይል ባለቤት የተባለችው ናይጄሪያ 6ኛ፣ ውጤታማ የኢኮኖሚ ገበያ ስርአት ባለቤት እንደሆነች የተነገረላት ኡጋንዳ 7ኛ፣ዜጎቿ ከእርስ በእርስ ግጭት ወጥተው በፍቅር ይኖሩባታል የተባለችው ሩዋንዳ 8ኛ፣ ህዝቧ ፈሪሃ አምላክ ነው የተባለችው ዚምባቡዌ 9ኛ ሲሆኑ በመጨረሻም የተረጋጋ የኢኮኖሚ ባለቤት የተባለችው አልጄሪያ 10ኛ ደረጃ ተሰጥቷል፡፡
 በአፍሪካ ተፅዕኖ ፈጣሪነት፡፡      

Published in ዜና
Page 17 of 17