አንድ የህንድ አፈ-ታሪክ እንዲህ ይላል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ወደ አመሻሹ ላይ አንድ የህንድ የመንደር አለቃ በድንገት ሴት ልጁ ወደምትተኛበት ድንኳን ጥልቅ ይላል፡፡ ለካ ሴት ልጁ ከሰፈሩ ቆንጆ ጎረምሣ ጋር ተቃቅፋ ተኝታ ኖሯል፡፡ ያ ጎረምሣ በሰፈሩ ዝነኛ ጀግና በመባል የሚታወቅም ነው፡፡ “እንግዲህ” አለ አባትዬው “ልጄን አቅፈህ እስከ መተኛት ከደረስህ በሥርዐቱ ልታገባት ይገባል፡፡ ሆኖም በሥርዓቱ እንድታገባትም ብፈቅድልህ እንዲሁ አልሰጥህም”
ጎረምሣው ጀግናም፤
“ምን ማድረግ አለብኝ ጌታዬ?” ሲል ጠየቀ፡
አባትየው፤
“ፈተና እሰጥሃለሁ፡፡ ያንን ፈተና ካለፍክ ልጄን እድርልሃለሁ”
ጎረምሣው ጀግና፤
“ለእሷ ፍቅር ስል ማናቸውንም ፈተና እቀበላለሁ!” አለ በሙሉ ልብ፡፡
አባትየውና ጎረምሣው ጀግና ተያይዘው መንደሩ ውስጥ ወደሚገኘው ሐይቅ ሄዱ፡፡ ክረምት ስለገባ ብርዱ እጅ ይቆርጣል፡፡ ቅዝቃዜው በድን ያደርጋል፡፡ ሁለቱም ደራርበው ለብሰዋል፡፡ ከፊታቸው በስተቀር የሚታይ ሰውነት የለም፡፡
ያ ሀይቅ ረግቶ በረዶ ሰርቷል፡፡ ጠርዙ ላይ ቆሙ፡፡
አባትየው፤
“ይህን በረዶ ከስክሰህ ገብተህ፣ ወደዚያኛው የሐይቁ ዳርቻ ዋኝተህ፣ ሁለቱን ኪሎ ሜትር ጨርሰህ፣ እዚህ ተመልሰህ ትመጣለህ፡፡ ስትመለስ ታላቅ ፌሽታ አደርግልሃለሁ፡፡ ከዛ ልጄን በሠርግ ታገባታለህ” ይለዋል፡፡
ጎረምሣው ጀግናም፤
“ለእሷ ያለኝ ፍቅር ይህንን ወንድነቴን (manhood) የሚፈታተነውን ፈተና እንዳልፍ እንደሚያበረታታኝ አልጠራጠርም” አለ፡፡
ከዚያም በረዶውን እየከሰከሰ ቆፍሮ በበረዶው ውሃ ውስጥ ዋና ጀመረ፡፡ ከሶስት ሰዓት በኋላ የጎረምሳው ጀግና ወሬ ደብዛው ጠፋ፡፡ እምጥ ይግባ ስምጥ የሚያቅ ሰውም ጠፋ፡፡ በስምምነታቸው መሠረት አባትየው ምሽቱ ዐይን እስኪይዝ ድረስ  ጠበቀው፡፡ ለአንዴም ለሁሌም እንደሄደ፤ እንዳበቃለት አወቀ፡፡ ያን ቅዝቃዜ ተቋቁሞ ያ ጎረምሣ ለፍቅረኛው አልደረሰላትም፡፡
የመንደሩ አለቃ፤ ለዚያ ጎረምሳ፣ ለልጁ እጮኛ ማስታወሻ ይሆን ዘንድ ሐይቁ ስም እንዲወጣለት አደረገ፡፡
ይኸው እስከዛሬ ያ ሐይቅ፤
“ደደቡ ሐይቅ” በመባል ይታወቃል፡፡
*       *      *
ደደቡ ሐይቅ ላለመባል ግራና ቀኝ ማየት፤ አርቆ ማስተዋል፤ ግትር አለመሆን ይጠበቅብናል፡፡ አንድና አንድ ነገር ላይ ብቻ አተኩረን፣ እሱም ላይ ግትር ሆነን አንችለውም፡፡ ምክንያቱም ከየአቅጣጫው የሚቦረቡሩንን ችግሮች ስራዬ ብለን ስለማናያቸው አወዳደቃችን አያምርምና ነው፡፡ የምናደንቀውና የምናወራለት ነገር ሳናስበው ከወደቀ “ወርቅ ከዛገ ብረት ምን ሊሆን ነው?” እንዳለው ቻውሰር፤ “ያመኑት ፈረስ ጣለ በደንደስ” ይሆንብናል፡፡
በድህነት ላይ ሙስና ተጨምሮ የት እንደሚያደርስ ማንም ጅል አይስተውም፡፡ “በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” ነው፡፡
“ከተማ ኢኮኖሚዋን በኮንትሮባንድ ላይ ከመሰረተች፤ አይዟችሁ፤ የጉምሩክም ሰራተኞች የደምቡን ጉርሻ ብቻ ነው የሚወስዱት” እያለ ይሳለቃል የአሜሪካው ተጓዥ ፀሀፊ ፒተር ማቴይሶን፡፡ ድርሻ ድርሻችንን ከወሰድን በኋላ፤ አገራችን እያደገች ነው ብሎ መለፈፍ ምን ያህል ቀላል እንደሚሆን መተማመን አያዳግትም፡፡ ትላልቆቹ አሳዎች የበሉትን በልተው ትናንሾቹ አሳዎች ላይ ቢላክኩ፤ የ “አይጥ በበላ ዳዋ ተመታ” ታሪክ ያህል አስገራሚ ነው፡፡ (እርግጥ ትናንሾቹ አሳዎችም ትርፍራፊ አልለቃቀሙም ማለት አይደለም፡፡) ህዝብም ያንን አይቶ “ወይ አገሬ!” የሚል ቁጭት ቢያሰማ አይገርምም፡፡ ቁጭቱን ሲለማመደው ግን “እገሌ ከበላው፣ እገሌ የበላው ይበልጣል፤ እንወራረድ!” እያለ የዕለት ኑሮ ያደርገዋል፡፡
የፈረንሳዩ ፀሀፊ ዣን ዣክ ሩሶ፤
“በፈጣሪ እጅ የተሰራው ፍፁም ነበር፡፡ እሰው እጅ ሲገባ ይነክታል ይነትባል” ይለናል፡፡ ወይም በእኛ ቋንቋ “ይቸከላል!”፤ ወይም የድሮው መሪ እንዳሉት “ብታምኑም ባታምኑም ሞተናል!” ያሉት ዓይነት ነገር ይሆናል፡፡
“ቀይ የመንገደኛ መብራት ሲበራ ማለፍ ክልክል ነው” የሚል የእንስት ድምፅ በየመንታ መንገዱ መብራቶች ዙሪያ ይሰማል፡፡ ማንም ባለመኪና ባይሰማውም የሴትየዋ ድምጽ፤ ከመንገዱ መብራት ጋር ብቅ ይልና እንደማንኛውም የድምፅ የአየር ብክለት፤ ማለትም እንደጡሩምባው፣ እንደ ጩኸቱ፣ እንደ አውቶብሱ ገዝጋዥ ድምፅ ወዘተ መወትወቱን ይቀጥላል፡፡ ባለመኪናውም አይሰማም፤ እግረኛውም አይሰማም፡፡ መንገዱም አይሰማም፡፡ በማይሰማ ማህበረሰብ መካከል የቴክኖሎጂ ፋይዳ ምን ያህል እንደሆነ ሳይጠቁመን አይቀርም፡፡
ሙስና ቁመቱና ዐርቡ እንዲሁም ስፋቱ አህጉራችንን ያጥለቀለቀ ነው፡፡ እንደተስቦ ድንበርተኞቹን አገሮች ያዳርሳል፡፡ የእኛ ውስጥ ውስጡን በተምችም፣ በምችም፣ በምሥጥም ጀምሮ አሁን አሁን መስረቅም ሆነ መንጠቅ አሊያም መዝረፍ፤ ወደ ብዝበዛ ተሸጋግሮ እንደ ናይጄሪያና ኬንያ ዐይን-ያወጣ የሆነበት ደረጃ ለመድረስ አንድ ሐሙስ የቀረን ይመስላል፡፡
ኦባፌሚ አዎሎዎ የተባለው የናይጄሪያ ጠበቃና ፖለቲከኛ፣ “ብዙዎቻችን የምንስማማበት አንድ ነገር አለ፡፡ ይኸውም በአፍሪካ ማህበረሰብ ሙስናን ማጥፋት አዳጋች ሥራ መሆኑ ብቻ አይደለም፡፡ ይልቁንም ዋናው ጣጣ፤ የማይቻል ዓላማ ማለማችን ነው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ የታችኛውን ሌባ የሚያስረው የላይኛው ሌባ መሆኑ ነው” ይለናል፡፡ እንግሊዞቹ who guards the guards እንደሚሉት መሆኑ ነው (ጠባቂዎቹን ማን ይጠብቃቸዋል እንደማለት ነው፡፡) ሥርዓቱ የፈቀደውን ሌብነት ያካሂዱ ዘንድ ዕድሉን አትከልክሏቸው፡፡ የሁላችንም የጋራ ሀብት ሌብነት ነውና ብንልም ያስኬዳል፡፡
ዛሬ መታሰርም እየቀለለ መጥቷል ይባላል፡፡ አንድ የአሥር ዓመት ፍርደኛ ያሉት ነገር እዚህ ላይ ተጠቃሽ ነው፡፡ “አይዟችሁ ብትታሠሩም የሰረቃችሁት ገንዘብ ያኖራችኋል፡፡” አንድ የዱሮ ባለሥልጣን እሥር ቤት ሲጎበኙ፤ “ይህ እሥር ቤት መታደስም፣ መስፋፋትም ይገባዋል፡፡ የወደፊት ቤታችን‘ኮ ነው!” አሉ፤ አሉ፡፡ አሉ ነዋ ነገራችን ሁሉ፡፡
The Strongest Poison ever known
Came from Caesar’s Laurel Crown
(auguries of Innocence)
“በዓለም ከታወቁት መርዞች፣ እጅግ በልጦ የተገኘው
ከቄሣር የወይራ ጉንጉን፣ ከዘውዱ የሚመጣው ነው” የሚለው ይሄ የዊሊያም ብሌክ ግጥም፤ የዓሳ ግማቱ ከጭንቅላቱ” ከሚለው የአማርኛ ተረት ጋር አብሮ-አደግ ነው፡፡ እኛ ስለዕድገት፣ ስለልማት ጧት ማታ እያወራን፣ ስለመልካም አስተዳደርና የሕግ የበላይነት እያወራን፤ ላይና ታች ሳይባል በየዕለቱ የሚሰማው የሙስና ጀብድ፤ አሳዛኝም አስደንጋጭም እየሆነ ነው፡፡ በከፍተኛ ደረጃ የሚወሳለት ዕድገት በዚህ ሁሉ ሙስና ማህል አቋርጦ እንዴት እንደሚሸጋገር አሳሳቢ ነው፡፡ እንዴት ያገሳ ይሆን ያሉት በሬ እምቧ ይላል፤ እንደሚባለው እንዳይሆን ዐይናችንን ገልጠን እንይ!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

           ከአወሊያ ት/ቤት ጉዳይ በተያያዘ መንግስት ጣልቃ ገብቷል በሚል በተፈጠረው ብጥብጥ ሳቢያ በሽብርተኝነት ተከስሰው እንዲከላከሉ ብይን የተላለፈባቸው ተጠርጣሪዎች የተከሳሽነት ቃላቸውን መስጠታቸውን ቀጥለዋል፡፡፡፡
ባለፈው ሰኞ በዋለው ችሎት፣ ሼህ መከተ ሙሄ እና ሣቢር ይርጉ የተከሳሽነት ቃላቸውን ለፍ/ቤቱ ሰጥተዋል፡፡ በጠዋቱ ችሎት የተከሳሽነት ቃላቸውን ከ2 ሰአታት በላይ በወሰደ ጊዜ ያሰሙት ሼህ መከተ ሙሄ፤ በብጥብጡ ወቅት ህዝቡን የማረጋጋት ሚና ከመወጣት ያለፈ ሁከትና ረብሻ አለማነሳሳታቸውን ተናግረዋል፡፡ ተከሳሹ እንደውም በፖሊስ ምርመራ ወቅት ከፍተኛ ቶርቸርና ስቃይ ይፈፀምባቸው እንደነበር ለፍ/ቤቱ አመልክተዋል፡፡  ከሰዓት በኋላ በቀጠለው ችሎት፣ ሣቢር ይርጉ የተከሳሽነት ቃሉን የሰጠ ሲሆን በህገመንግስቱ የተደነገጉትን የሃይማኖት እኩልነት እና የሰዎችን የግል እምነትና አስተሳሰብ እንደሚያከብር ገልፆ፤ እስላማዊ መንግስት ይቋቋም በሚል አስተሳሰብ አለመንቀሳቀሱንም አስረድቷል፡፡ ቤተሰቦቹ የክርስትና እምነት ተከታዮች መሆናቸውን በመጠቆምም ከኔ ሌላ ሃይማኖት አይኑር የሚል አመለካከት እንደሌለው ለችሎቱ አስረድቷል፡፡
ተከሣሹ አወሊያን አስታኮ በተፈጠረው ብጥብጥ አለመሳተፉን፣ በሚኖርበት አካባቢ ብጥብጥ እንዳይነሳ ህዝበ ሙስሊሙን የማረጋጋት ሥራ ሲሰራ እንደነበር አመልክቷል፡፡ በምርመራ ወቅትም በተለያየ መንገድ ቶርች ከመደረጉም በላይ ስቃይ የታከለበት ምርመራ እንደተፈፀመበት ለፍ/ቤቱ አመልክቶ፤ ፍ/ቤቱ ንፅህናውን አረጋግጦ በነፃ እንዲያሰናብተው ጠይቋል፡፡
በማክሰኞው ጠዋት ችሎት ተከሣሾች፣ ጠበቆች እንዲሁም ቁጥራቸው በመቶዎች የሚገመት የተከሳሽ ቤተሰቦችና ወዳጆች በችሎቱ ቢታደሙም አቃቤ ህግ ባለመቅረቡ የእለቱ ችሎት እንደማይኖር የገለፀው ፍ/ቤቱ ረቡዕ እለት በሚውለው ችሎት አቃቤ ህግ ለምን በሰአቱ እንዳልደረሰ ከሚገልጽ ምክንያት ጋር ይቅረብ ሲል ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡
ረቡዕ 4፡30 ላይ የተጀመረው ችሎትም በመሃል መብራት በመጥፋቱ ተቋርጦ ከሰአት በኋላ የቀጠለ ሲሆን በእለቱ መሃመድ አባተ እና አህመድ ሙስጠፋ የተከሳሽነት ቃላቸውን ለፍ/ቤቱ ሰጥተዋል፡፡
በመዝገቡ 8ኛ ተከሣሽ የሆነው መሃመድ አባተ፤ ሐምሌ 7 ቀን 2004 በአንዋር መስጊድ ለተሰበሰበው ህዝብ በአወሊያ መስጊድ ፖሊስ ሙስሊሞችን ስለገደለ፣ ፀሎትና ሶላት እንዲደረግ መልዕክት አስተላልፎ እንደነበር በችሎቱ ገልፆ፤ በእለቱ የሞተ ሰው አለመኖሩ መረጃ ሲደርሰው ወዲያውኑ ማስተባበሉን ተናግሯል፡፡ በቀጣይ ባለው ሂደትም ህዝቡን የማረጋጋት ስራ ሲሰራ እንደነበር ለፍ/ቤቱ ያመለከተው ተከሣሹ፤ ህዝቡ በስሜታዊነት ተነሳስቶ ከፖሊስ ጋር ግጭት እንዳይፈጥር ጥረት ሲያደርግ እንደነበር አስታውቋል፡፡
ሃይማኖትን ሽፋን በማድረግ ፖለቲካዊ ግብ ለማሣካት በህቡዕ አልተንቀሳቀስኩም ያለው ተከሣሹ፤ መንግስት ሃይማኖትን እየከፋፈለ ነው ብሎ በፈቲህ መስጊድ ለህዝብ አለመናገሩንም አስታውቋል፡፡
ሌላው የተከሣሽነት ቃሉን ለችሎቱ የሰጠው አህመድ ሙስጠፋ በበኩሉ፤ “ሃይማኖታዊ መንግስት የማቋቋም አላማ አልነበረኝም፤ አክራሪነትንም አላራመድኩም” ሲል ቃሉን ሰጥቷል፡፡ በተጨማሪም ወደ ውጭ ሀገር ሄዶ የወሰደው ስልጠና የአመፃ ሣይሆን ስለሃይማኖት መከባበርና መቻቻል እንደሆነ ለችሎቱ አስረድቷል፡፡ ከውስጡ በተወሰደ ሃሳብ ውይይት ተካሂዶበታል የተባለው መጽሐፍም ስለ ስልጣኔና የህዳሴ ጉዞ ሣይንሳዊ ትንታኔ የተሰጠበት እንጂ ሃይማኖታዊ መንግስትን ስለማቋቋም የሚያወሣ አይደለም ሲል ቃሉን ሰጥቷል፡፡
አቃቤ ህግ በተከሳሾች ላይ ማስረጃ ቀርቦ ብይን ከተሰጠ በኋላ የተከሳሽነት ቃል መሰጠቱ የስነ ስርአት ህጉን የተከተለ አይደለም ሲል ለችሎቱ አቤቱታ  ያቀረበ ሲሆን የተከሳሽ ጠበቆች በበኩላቸው፤ “አቃቤ ህግ ተከሣሾችን አቋርጦ ጥያቄ ያቀረበው ሃሳባቸውን ለማቋረጥ ነው፤ ጥያቄውም ተገቢ አይደለም” ሲሉ ተቃውመዋል፡፡ ችሎቱም የክርክር ሂደቱ የስነስርአት ህጉን የጣሰ አይደለም ሲል የአቃቤ ህግን ጥያቄ ውድቅ አድርጐ የተከሳሽነት ቃል የመስማት ሂደቱ እንዲቀጥል ብይን ሰጥቷል፡፡ ሃሙስ እለት በነበረው ችሎትም አቃቤ ህግ በድጋሚ ባቀረበው ጥያቄ፤ እያንዳንዱ ተከሳሽ በተመሳሳይ ፍሬ ነገር ላይ ቃሉን እንዲሰጥ መደረጉ ሂደቱን ያራዘመ ነው፤ ለቃል መስጫ ቢበዛ 25 ደቂቃ ተብሎ ይገደብልኝ ሲል አመልክቷል፡፡ ፍ/ቤቱ በሰጠው ብይንም በስነስርአት ህጉ የሰአት ገደብ ሊደረግ ይገባል የሚል ስላልሠፈረ ሂደቱ ባለበት ይቀጥል ሲል በይኗል፡፡  
በመዝገቡ 10ኛ ተከሳሽ የሆነው ሙራድ ሽኩር በእለቱ በሰጠው የተከሳሽነት ቃል “በህገ መንግስቱ የሰፈረውን የእምነት ነፃነት አልተቃረንኩም፣ ለማስከበር ተንቀሳቅሻለሁ እንጂ፣ አህባሽ በመንግስት ታግዞ እኔ ላይ በግድ አስተምህሮቱን ለመጫን ያደረገውን ጥረት ተቃውሜያለሁ፤ ይህን በመቃወሜ ሃይማኖታዊ መንግስት እንዲቋቋም እንደፈለግሁ መታሰብ የለበትም፣ አወሊያ ዘወትር አርብ ሲካሄዱ በነበሩት አብዛኛዎቹ ስብሰባዎች ላይ ተሳትፌያለሁ፤ በወቅቱም ችግር እንዳይፈጠር ህዝቡን የማረጋጋት ስራ ስሰራ ነበር” ሲል አስረድቷል፡፡ በአቃቤ ህግ የታሰሩ የቡድኑን አባላት በህገ ወጥ መንገድ ለማስፈታት ገንዘብ አሰባስቧል ተብሎ ለቀረበበት ክስም ለዘካ በሚውል ከአንድ ግለሰብ 50ሺህ ብር መቀበሉንና ለታሳሪ ቤተሰቦች ችግር መውጫ ከማከፋፈሉ በቀር አንዳችም የማስፈታት እንቅስቃሴ አለማድረጉን አስታውቋል፡፡ በፖሊስ ምርመራ ወቅት ስቃይ የታከለበት ምርመራ እንደተካሄደበትም ተከሳሹ ገልጿል፡፡
“የሙስሊሙ የመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ” አባል አለመሆኑንና የሚዲያ ባለሙያ እንደሆነ የጠቆመው 11ኛ ተከሳሽ አቡበከር አለሙ በበኩሉ፤ አዲስ አድማስን ጨምሮ በተለያዩ ሚዲያዎች የተለያዩ ፅሁፎች ለአንባቢ ያቀርብ እንደነበር ገልጿል፡፡ በመንግስትና በሃይማኖት መካከል ስላለው ግንኙነት የተቸባቸው ጽሁፎች እንዲሁም በቤቱ በተገኘ የእለት ተእለት ማስታወሻ ደብተሩ ላይ የሰፈሩ ጽሁፎች እንደማስረጃ መቆጠራቸውን ጠቅሶ እነዚህን ይዞ መገኘቱ በሽብር ሊያስጠረጥረው እንደማይገባ ተናግሯል፡፡
በምርመራ ወቅት ድብደባን ጨምሮ በተለያዩ የማሰቃያ ዘዴዎች በግድ ቃሉን እንዲሰጥ መደረጉን የገለፀው ተከሳሹ፤ “ኮሚቴው ህገ ወጥ ነው፣ እስላማዊ መንግስት የመመስረት ፖለቲካዊ ግብ ነበረኝ” እንዲል መገደዱን አመልክቶ፤ “እኛ ተራ የሆነ ወዳጅነት እንጂ በህቡዕ አልተደራጀንም፤ በግሌም እስላማዊ መንግስት እንዲመሰረት ፍላጎት የለኝም” ብሏል፡፡ ይህን በመሰለ አስገዳጅ ሁኔታ ለፖሊስ የሰጠው ቃል እንደ ማስረጃ ተቀባይነት እንዳያገኝ ፍ/ቤቱን ጠይቋል፡፡
የግል ማስታወሻ ደብተሩ ላይ የሰፈሩ ጽሁፎች ፍሬ ሃሳብን በተመለከተ ለፍ/ቤቱ ያብራራው ተከሳሹ፤ ባለው እውቀትና መረጃ የፀሐፊነት ሙያውን ተጠቅሞ ስለምስራቅ አፍሪካ ቀንድ ፖለቲካ እንዲሁም ስለእስላማዊ መንግስት ምንነት የሚተነትኑ መፅሃፍት ለማዘጋጀት የተለያዩ ቢጋሮች አዘጋጅቶ እንደነበርና ይህን መጽሃፍ ማዘጋጀቱ እስላማዊ መንግስት እንዲቋቋም እንደመሻት ሊያስቆጥርበት እንደማይገባ በሰጠው የተከሳሽነት ቃል አመልክቷል፡፡ አክሎም “ይህን የግል ጽሁፍ ማንም ሰው አላነበበውም፤ በኔ የማስታወሻ ደብተር ላይ በሰፈሩት ሃሳቦች ተነሳስቶ የሽብር ድርጊት የፈፀመ የለም” ሲል ተናግሯል፡፡
“የሙስሊሞች ጉዳይ” የተሰኘ መጽሄት በህጋዊ መንገድ  ከሌሎች ግለሰቦች ጋር በአክሲዮን ማቋቋማቸውን የጠቆመው ተከሳሹ፤ መጽሄቱ ስለ እስላማዊ መንግስት መመስረት ያንፀባረቀበት ጊዜ የለም ብሏል፡፡ “መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ ገባ ብሎ መጠየቅና መተቸትም የሽብርተኝነት ድርጊት ለመፈፀም መዘጋጀት አይደለም” ሲል አክሎ ገልጿል፡፡
ቀደም ሲል ተከሳሾች በማረሚያ ቤቱ እየተፈፀመብን ነው ያሉትን በደል ለፍ/ቤቱ በዝርዝር ማቅረባቸውን ተከትሎ ስለጉዳዩ ማረሚያ ቤቱ ቀርቦ እንዲያስረዳ ፍ/ቤት በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት፣ የማረሚያ ቤቱ የጥበቃ ደህንነት ኃላፊ ዋና ሱፐር ኢንተንደንት ማሞ ተክሉ ችሎት ቀርበው ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ከተከሳሾች የቀረቡትን አቤቱታዎች ኃላፊው በዘጠኝ ነጥቦች አደራጅተው ምላሽ የሰጡ ሲሆን ከሌሎች ታራሚዎች በተለየ መልኩ ጠያቂ ቤተሰቦቻችን ይንገላታሉ፤ ሽብርተኛ እየተባሉም  ይሰደባሉ ለተባለው “ውንጀላው ሃሰት ነው፤ በእንክብካቤና በተለየ መልኩ በአክብሮት ነው የምናስተናግደው፤ ይህን ፍ/ቤቱ ባለሙያ ልኮ መታዘብ ይችላል” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ አሸባሪ እየተባልን እንሰደባለን ለሚለውም ተቋሙ ያልተፈረደባቸው ሰዎች በንፁህ የመገመት መብት እንዳለቸው ይገነዘባል ሲሉ በተከሳሾች የክስ ዋራንት ላይ በሽብር የተከሰሱ ይላል እንጂ የስድብ ቃል አልወጣንም ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
የግራ ቀኙን ክርክር ያዳመጠው ፍ/ቤቱም፤ ተከሳሾች የማረሚያ ቤቱን ደንብ በሚገባ እንዲገነዘቡ ምክር በመስጠት፣ ችግሮቹ በአስተዳደራዊ ውሳኔ እልባት እንዲያገኙ ወስኗል፡፡
አቃቂ በሚገኘውና የቀድሞ የቅንጅት አመራሮች ጉዳይ በታየበት አዳራሽ እየተካሄደ ባለው የፍርድ ሂደት፣ የተከሳሽነት ቃል መሰማቱ ቀጥሏል፡፡

የህዳሴ ግድብ የመሰረት ድንጋይ የተጣለበትን ሶስተኛ ዓመት ክብረበዓል ለመታደም ከበርካታ የሙያ አጋሮቼ ጋር ጉዞ ወደ ግድቡ ተጀምሯል፡፡
ምንም እንኳን አብዛኛው ጋዜጠኛ ጉዞው በአሶሳ በኩል እንዲሆንለት ሃሳብ ቢያቀርብም ከመብራት ሃይል ተመድበው የመጡት አስተባባሪዎች እጅ ጥምዘዛ ግን ጉዟችን በጐጃም መንገድ እንዲሆን አደረገን፡፡ ጉዟችን ቀጥሎ ምሳ ደብረ ማርቆስ ሆነ፡፡ ተወላጆቿ “ዴንማርክ” እያሉ የሚጠሯት የቀድሞዋ “መንቆረር” የአሁኗ ደብረማርቆስ ስንደርስ አዳርም እዚያው መሆኑን አወቅን፡፡ ታዲያ የአዳር እና የመመገቢያ ቦታም የሚመረጥልን በእነዚሁ አስተባባሪዎች ነበር፡፡
ምሳ ሐበሻ ምግብ ቤት እንድንመገብ ቢነገርም እኔና ሌሎች ጓደኞቼ አልጋ ከያዝንበት “ዴሉክስ ገስት ሀውስ” ጀርባ ወደሚገኘው ፓራዳይዝ ሬስቶራንት አመራን፡፡ ምሳ ለማዘዝም የምግብ ዝርዝር የለበትን ሜኑ አነሳን፡፡ በዚህ ጊዜ ነበር አስገራሚውን የምግብ ስም ዝርዝር ያየሁት፡፡ ከሁሉም በላይ ያስገረሙኝን ምግቦች ስም ዝርዝር እና የስሞቹን ምክንያት ለማወቅ ጉጉቴ ጨመረ፡፡ ህዳሴ ሽሮ፣ ኑሮ በዘዴ፣ ባትኖርም ትኖራለህ፣ ፍቅር ሽሮ፣ አፋታሽኝ፣ ማይ ቾይዝ እያለ ይቀጥላል… የምግቡ ዝርዝር፡፡
እኛ ርቦን ስለነበር ለሶስት ሰው አሳምሮ ይበቃል የተባለለትን “ማይ ቾይዝ” የተሰኘ ጣፋጭ የፆም ምግብ አዘዝን፡፡ ተመግበን ከጨረስን በኋላ በሚገርም ቅልጥፍናና ትህትና ተፍ ተፍ እያለ ያስተናገደንን ወጣት ቢኒያምን ጠርቼ ስለምግቦቹ አሰያየም እንዲያወጋን ጠየቅሁት፡፡ ወጣት ቢኒያም ጌታቸው እድገቱ አዲስ አበባ በተለምዶ ዳትሰን ሰፈር እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ነው፡፡ ሰሜን ሆቴል ውስጥ ረዘም ላለ ጊዜ በአስተናጋጅነት መስራቱን ይናገራል፡፡ “ህዳሴ ሽሮ”
እንደ ቢኒያም ገለፃ፣ ህዳሴ ሽሮ በፓራዳይዝ ሆቴል ስፔሻል ተብሎ ከሚጠራው “ማይ ቾይዝ” ቀጥሎ ተወዳጅ ምግብ ነው፡፡ ከህዳሴው ግድብ የመሰረት ድንጋይ መጣል በኋላ ህዝቡ ስለ ህዳሴው ግድብ በስፋት ያወራ በነበረበት ጊዜ ስም የወጣለት ልዩ ጣዕም ያለው ምግብ እንደሆነ አጫውቶኛል። በፓራዳይዝ ሬስቶራንት ብቻ ይሰራል የተባለው “ህዳሴ ሽሮ”፤ አሰራሩ እና አቀራረቡ የህዳሴውን ግድብ ዲዛይን የተከተለ መሆኑ ይበልጥ አስገራሚ ያደርገዋል፡፡ በትሪ የተዘረጋ እንጀራ ላይ ዙሪያውን ሽሮ ይደረግበታል፡፡ ከዚያም መሀሉ ህልበት (ስልጆ/የተሰኘው የፆም ምግብ ማባያ ይጨመራል፡፡ እንደወጣቱ ገለፃ፤ ሽሮው ዙሪያውን መሆኑ የግድቡን ዙሪያ የሚያሳይ ሲሆን፤ ነጩ ህልበት(ስልጆ) ውሃውን የሚያመላክት ነው፡፡ በተጨማሪም የአበሻ ጐመን፣ ቃሪያ፣ የተቀቀለ ድንችና ሰላጣ ዙሪያውን ለአይነት የሚጨመርበት ሲሆን፤ በምግቡ አራት ቦታዎች ላይ አራት ኮለኖች አሉት፡፡ ይህም የግድቡን አራት ማዕዘናት ለማሳየት ነው፡፡
አራቱ የምግቡ ኮለኖች በቲማቲም በቅርፅ የተሰሩ ናቸው፡፡ ይህ ምግብ ጣዕም ብቻ ሳይሆን ጥበብም የተሞላበት በመሆኑ በተመጋቢዎች ተመራጭ እንደሆነ ቢኒያም ይናገራል፡፡ “በየወቅቱ በሚከሰቱ ሁነቶች ብዙ የልብስ፣ የምግብና መሰል ቁሳቁሶች ስያሜ ይወጣል” የሚለው ወጣቱ አስተናጋጅ፣ በምሳሌነትም ከኢትዮጵያ ሚሌኒየም ጋር ተያይዞ የወጡ የቡቲክ፣ የምግብ ቤት፣ የውበት ሳሎኖችና ሌሎች ድርጅቶችን ጠቅሷል፡፡ ኦባማ የአሜሪካ ፕሬዚደንት ሆነው ሲመረጡ፣ አንዳንድ የንግድ ሱቆች በስማቸው መሰየማቸውን ያስታወሰው አስተናጋጁ፤ ከነዚህም መካከል ባህርዳር ከተማ ውስጥ የሚገኘውን “ኦባማ ካፌ”ን በምሳሌነት አንስቷል፡፡

“ባትኖርም ትኖራለህ”
በሜኑው ላይ ትኩረትን ከሚስቡት የምግብ አይነቶች አንዱ “ባትኖርም ትኖራለህ” የተሰኘው የምግብ አይነት ነው፡፡ ለምን ስያሜው እንደተሰጠው የጠየቅሁት ቢኒያም፤ “እንደምታውቂው እዚህ አገር ላይ በጣም ሀብታም እንዳለ ሁሉ በጣም ድሀ የሆነም በገፍ አለ፡፡ ይሁን እንጂ የምግቡ አይነት ቢለያይም ሀብታሙም ድሀውም ሳይበሉ አያድሩም” ይላል፡፡ “ባትኖርም ትኖራለህ” የተሰኘውም ምግብ ከድንች ቅቅልና ከተወቀጠ ተልባ የሚሰራ ሲሆን ዋጋው በጣም ዝቅተኛ በመሆኑ ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው የሚዘጋጅ እንደሆነ ገልፆ፤ ይህ ስያሜ “ባይኖርህም ትኖራለህ፤ ሳትበላ አታድርም” ለማለት እንደተሰየመ አጫውቶኛል፡፡

“ኑሮ በዘዴ”
ይህ የምግብ ዓይነትም ኢኮኖሚን መሰረት ያደረገ ስያሜ የተሰጠው መሆኑን አስተናጋጁ ይናገራል። ምግቡ በአገልግል ተዘጋጅቶ እንደ በየአይነቱ የሚቀርብ ሲሆን ዋጋው በጣም ዝቅተኛ በመሆኑ። ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው ሰዎች የሚያዘወትሩት ነው። ዋጋው ዝቅተኛ ቢሆንም ግን ጥራቱን የጠበቀ በመሆኑ ተወዳጅም ነው፡፡ “ሰው ኑሮው እየከበደው ስለመጣ እነዚህን ምግቦች በመመገብ ኑሮውን በዘዴ ለማለፍ ይጠቀምበታል” ብሏል - አስተናጋጁ፡፡

“ማይ ቾይዝ”
“ማይ ቾይዝ” ለእኔና ለሁለት ጓደኞቼ ቀርቦልን ለሶስት ያጣጣምነው ግሩም ጣዕም ያለው ምግብ ነው፡፡ የሚሰራው በአካባቢው ከሚገኙ እንደ የአበሻ ጐመን፣ ድንች ቲማቲምና መሰል አትክልቶች ነው። በጣም ጣፋጭና በከተማዋ በፓራዳይዝ ሆቴልና በሆቴሉ ሼፍ ብቻ የሚዘጋጅ መሆኑን ቢኒያም ጌታቸው ያስረዳል፡፡ “እስካሁን ከመጣችሁ ጀምሮ ለዚህ ሁሉ ሰው ሳቀርብ የነበረው ማይ ቾይዝንና ህዳሴ ሽሮን ነው” የሚለው አስተናጋጁ፤ ምግቡ ጣፋጭና መጠኑም በርከት ያለ በመሆኑ፣ በአብዛኛው ሁለትና ሶስት ሆነው የሚመጡ ቤተሰቦችና ጓደኛሞች እንደሚያዘወትሩት አጫውቶናል፡፡

“ፍቅር ሽሮ”
በአብዛኛው የምግብ ገበታ ላይ በመቅረብ እንደ ሽሮ እድለኛ የለም ባይ ነው፤ አስተናጋጁ። ይሁን እንጂ ሁልጊዜ አንድ አይነት ሽሮ ሲቀርብ አሰልቺ ይሆናል፤ ሽሮን ከአሰልቺነት አውጥቶ በፍቅር የሚበላና የሚወደድ ለማድረግ የተዘየደ ዘዴ እንዳለ አጫውቶኛል፡፡ ሽሮው በተዘረጋው እንጀራ ላይ ዳር እስከዳር ከተቀባ በኋላ፣ የተቀላቀለ እና የተቀቀለ አትክልት በሽሮው ላይ ይጨመርበታል። በመቀጠልም በአራት ማዕዘን ቅርፅ እንጀራው ይታጠፍና ይቀርባል፡፡ ጣዕሙም እጅግ ግሩም ይሆናል፡፡ “ይሄን ሽሮ ከአሰልቺነት ተላቃ በፍቅር የምትበላ ትሆናለች” ይላል - ቢኒያም፡፡ በነገራችን ላይ በጥር ወር አካባቢ ለጥምቀት ፌስቲቫል ጐንደር ከተማ በነበርኩበት ጊዜ፣ አፄ በካፋ ሆቴል ውስጥ “ሽሮ በአትክልት” በሚል ስያሜ አንድ ምግብ መመገቤን አስታውሳለሁ፡፡ አሁን ስሟን ቀይራ “ፍቅር ሽሮ” ተሰኝታ በደብረማርቆስ ተገናኘን እንጂ።

“አፋታሽኝ”
አንድ አባወራ ሁሌ ፓራዳይዝ ሆቴል እየመጣ ራት ይመገብ ነበር፡፡ በዚህም የተነሳ ሁሌ ከሚስቱ ጋር ይጋጫል፡፡ ምክንያቱም ቤቱ ውስጥ ራት አይመገብም፡፡ ሚስት ክፉኛ ስጋትና ጥርጣሬ ውስጧን ይንጠዋል፡፡ “ባሌ እራት የሚበላበትና የሚያመሽበት ሌላ ቤት መስርቷል” የሚል ስጋትና ጥርጣሬ፡፡ ነገሩ ሲደጋገምባት ሚስት የፍቺ ጥያቄ ታቀርባለች፡፡ ባል ግን ከዚህ ምግብ መላቀቅ አልቻለም፡፡ ሚስት ባል የነገራትን አምና መቀበል ባለመቻሏ ትዳሯን በፍቺ አፈረሰች፡፡ ባልም ብቻውን ቀረ፡፡ ሚስቱን በፈታ በነጋታው ማታ፣ መሀል ላይ ቆሞ “ማነህ አስተናጋጅ፤ ያቺን አፋታሽኝን አምጣልኝ” በማለት ከሚስቱ ያፋታውን ምግብ ያዛል። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የምግቡ ስም “አፋታሽኝ” ሆኖ መቀጠሉን አስተናጋጁ አውግቶኛል፡፡ “አፋታሽኝ” ከካሮት፣ ከድብልቅ ሰላጣ፣ በጣም ካልበሰለ ድንችና ሌሎች አትክልቶች የሚዘጋጅ ሲሆን ጣዕሙ አሪፍና ዋጋውም ኪስን የማይጐዳ በመሆኑ በብዙ ተመጋቢዎች ይመረጣል፡፡ በአካባቢው ባሉ ሌሎች ሆቴሎች አስገራሚ ስም ያላቸው ምግቦች ይኖሩ እንደሆነ የጠየቅሁት ቢኒያም፤ ማይ ቾይዝ፣ ህዳሴ ሽሮና አፋታሽኝ በሌሎች የትም ሆቴሎች እንደሌሉ ገልፆ አንድ ሆቴል “አገልግል” የተሰኘውንና በሁሉም ሆቴል የሚገኘውን ምግብ “ማሰሮ” በማለት ስሙን ለመቀየር ሞክረዋል፤ ሆኖም በይዘቱ ላይ ለውጥ አላመጡም ሲል አጫውቶኛል፡፡ 

Published in ህብረተሰብ


የኢትዮጵያን እና የሱዳንን ግንኙነት እንዴት ይገልፁታል?
የሁለቱ አገሮች ግንኙነት ማብራሪያ የሚፈልግ ጉዳይ አይደለም፡፡ ምክንያቱም እየኖርነው ያለ ጉዳይ ነው፡፡ የሁለቱ አገራት ህዝቦች እጅግ የተቀራረበ ታሪክ እና ባህል ያላቸው ናቸው፡፡ ይብራራ ከተባለም ግንኙነቱ ረጅም ዘመናትን የተሻገረ፣ጥልቅ የሆነ እና ብዙ አቅጣጫዎች ያሉት ነው፡፡ ብዙ ጊዜ የሚታየው በፖለቲካዊው ጐኑ ቢሆንም ግንኙነቱ ከዛ ያለፈ ነው፡፡ በታሪክ ትስስር አለ፣በጂኦግራፊ ጐረቤታሞች ነን፣ብዙ የምንጋራቸው ነገሮች አሉን፡፡ በባህል ካየነው የምንኖረው በአንድ ክፍለ አካባቢ ነው፡፡ ወንዝ እንጋራለን፣ በአንድ ሰማይ ስር እየኖርን ነው፡፡ እነዚህ የጋራ የሆኑ ነገሮች ባህሪያችን ላይ ተመሳሳይ እንድንሆን የሚያደርግ ተጽእኖ ይኖራቸዋል፡፡ የአካባቢውን ታሪክ የሚያጠኑ ሱዳን እና ኢትዮጵያ የሚጋሩት የኋላ ታሪክ እንዳላቸው ይናገራሉ፡፡ ህዝቦቹ የተሳሰሩ ናቸው፡፡
አንቺ እና ልጄን እንደሁለት አገር ዜጋ መለየት ይከብዳል፡፡ አሁን እዚህ ብትሆን በደንብ ትረጂው ነበር፡፡ በቅርቡ አፍሪካ ህብረት ሊፍት ውስጥ አንዲት ኢትዮጵያዊት በአማርኛ አናገረችኝ። ይቅርታ አማርኛ አልችልም ስላት፣ሱዳናዊ ነህ አለችኝ፡፡ በፖለቲካው ካየን ብዙ የምንጋራቸው ጉዳዮች አሉን፡፡ በተለይ ከቀድሞው ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ ጊዜ ጀምሮ ጥሩ ግንኙነቶች አሉ። ፕሬዚዳንት አልበሽር ወደ ኢትዮጵያ ተደጋጋሚ የስራ ጉብኝት ያደርጋሉ፡፡ አንዳንዶች እንዲያውም አልበሽር ካርቱም ከሚያሳልፉት ጊዜ ይልቅ አዲስ አበባ የሚያሳልፉት ይበዛል ይላሉ፡፡ የሚቀጥለው ሳምንትም የጣና ፎረም ላይ ለመካፈል ይመጣሉ። የፖለቲካ ግንኙነቶቹ በጠንካራ መሠረት ላይ ይገኛሉ፡፡ ስምምነቶችን በተግባር ለማዋል እየሠራን ነው፡፡
ይህ ሁሉ ዝምድና ቢኖርም ቪዛ ግዴታ ነው፡፡ እዚህ ላይ ምን ታስቧል?
ምን ችግር አለ?
ለምሳሌ ኬኒያና ኢትዮጵያ ቪዛ አይጠይቁም----
ጥያቄሽ ሌላ ጥያቄ በውስጡ ከሌለው በስተቀር አሁንም እጅግ የተቀራረበ ዝምድና እና ጉርብትና አለን፡፡ የቪዛ ጉዳይ ከአገር አገር ይለያያል፡፡ ከድንበር ድንበር ይለያያል፡፡ የኢትዮጵያና የሱዳንን ካየን 800 ኪሎ ሜትር የሚጠጋ ድንበር እንጋራለን፡፡ ድንበሩ እስከአሁን አልተለየም፡፡ እንዲያም ሆኖ በሁለቱ ህዝቦች መካከል ያለውን ግንኙነት ለማፋጠን በቅርቡም ስምምነት ተደርጓል፡፡ ሁለቱም አገሮች ከልብ እየሠሩ ነው፡፡
በምን መልክ ?
ቀስ በቀስ ቪዛ ማንሳት ላይ እንመጣለን። ዲፕሎማቲክ ፓስፖርት ለያዙ እና ለመንግስት ሃላፊዎች የቪዛ ጥያቄ የለም፡፡ ቢዝነስ ፓስፖርት ያላቸውም ካርቱም ሲደርሱ ቪዛ ያገኛሉ። በአጠቃላይ ቪዛ ማንሳት የሚለውን ግን ከሚመለከታቸው የኢትዮጵያ መንግስት የስራ ሃላፊዎች ጋር እየተማከርንበት ያለ ጉዳይ ነው፡፡ ፍላጐቱ አለ፡፡
ሁለቱን አገሮች በአውራ ጎዳና  ለማገናኘት የታሰበውስ ምን ላይ ደርሷል?
ከገዳሪፍ፣ ጋላባት የሚመጣው መንገድ አልቋል። የሁለቱን አገራት ህዝቦች እያገለገለ ነው፡፡ በየቀኑ ከካርቱም አዲስ አበባ የሚመጡ አውቶቡሶች አሉ። አሶሳ ኩርሙክ በኢትዮጵያ በኩል ስራው አልቋል። ከሱዳን በኩል ከደማዚን ኩርሙክ የሚያገናኘው እየተሠራ ነው፡፡ በቅርቡ ተገናኝቶ ስራ ይጀምራል። ሌላው ከሁመራ የሚያገናኘውም ሲያልቅ በተለያዩ ሶስት አቅጫዎች ኢትዮጵያና ሱዳን በአውራ ጐዳና ይገናኛሉ፡፡ በሶስት የተለያዩ መንገዶች የሚገናኙ የአፍሪካ አገሮች የሉም፡፡ ሱዳንና ኢትዮጵያ ይህን ያሟላሉ፡፡ ይህ ደግሞ የሰዎችን ህይወት የሚለውጥ ነው፡፡ መንገዶቹ ሲገናኙ ኢትዮጵያ ፖርት ሱዳንን መጠቀም በምትችልበት ሁኔታ ላይ ለመስራት እያሰብን ነው፡፡
የሁለቱ አገሮች ድንበር ያልተሠመረ ነው፡፡ ለማስመር እየተሠራ ያለው ስራ በምን ሁኔታ ላይ ይገኛል?
ቅድም እንዳልኩት ኢትዮጵያ እና ሱዳን ረጅም ድንበር ተጋሪዎች ናቸው፡፡ የሱዳን አራት ግዛቶች እና የኢትዮጵያ ሶስት አካባቢዎች የዚህ ድንበር አካል ናቸው፡፡ የማካለሉ ጉዳይ በሁለቱ አገሮች መሀል ረጅም ጊዜ የወሰደ ነው፡፡ የጋራ የድንበር ኮሚሽኑ ላይ ሁለቱም አገሮች በብዙዎቹ ጉዳዮች ላይ ተስማምተው ቦታዎች ለማካለል ዝግጁ ናቸው። ያላለቁና ድርድር እና ውይይት የሚፈልጉ የተወሰኑ ቦታዎች አሉ፡፡ ኮሚቴው ስራውን አላጠናቀቀም፣ ፊርማም አልተፈረመም፡፡
በሂደቱ ላይ ያሉ ችግሮች ምንድን ናቸው?
ፖለቲካዊ ሳይሆን ቴክኒካዊ ችግሮች አሉ፡፡
ቴክኒካዊ ችግሮች ምን ማለት ነው?
ጉዳዩ ሁለት ገጽታዎች አሉት፡፡ አንዱ ቲዎሪ ነው፡፡ ሌላው ፖለቲካዊ ነው፡፡ የቴክኒክ  ቡድኑ በንድፈ ሃሳብ ደረጃ የሠራቸውን ስራዎች ቦታው ላይ ወርዶ ለመስራት ሲሞክር፣አንደኛ የቦታዎቹ አቀማመጥ እጅግ አስቸጋሪ ነው፤ ተራራ ይወጣል፣ ሸለቆ ይገባል --- የመሳሰሉት፡፡ ሁለተኛ ቴክኒካሊ ጉዳዩ በጣም ጥንቃቄ የሚፈልግ ነው፡፡ በመርህ ደረጃ ሁለቱም ተስማምተዋል - ለፖለቲካ፣ ለፀጥታ እና ለሌሎች ጉዳዮች፡፡ ስምምነት ባልተደረገባቸው ቦታዎች ላይ አሁንም ውይይቱና ድርድሩ አላለቀም። ሁለቱም ፍቃደኞች ስለሆኑ ይፈታል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር በተያያዘ በሱዳንም ሆነ በኢትዮጵያ በኩል ያሉ ጉዳዮችን ማስተናገዱ ፈታኝ ነው፡፡ ስራው ገንዘብ ይፈልጋል፡፡ ገንዘብም ችግር ነው፡፡ ነገር ግን ከሁለታችን ውጪ ማንም እንዳይገባ ተስማምተናል፡፡ ሁለቱም አገሮች ፈተናውን ለመወጣት እየሞከሩ ነው፡፡  ከየትኛውም ወገን ማንንም ሳይጎዱ ጉዳዩን ለመቋጨት ፍላጎት አላቸው፡፡
ኢትዮጵያ ለሱዳን መሬት ቆርሳ ሰጥታለች የሚሉ ወገኖች  አሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ?
ለምን ትሰጣለች?
እርስዎ ምን ይላሉ ?
ለምን? ለምን? ኢትዮጵያ ለምን መሬት ትሰጠናለች? በመጀመሪያ ከኢትዮጵያም ሆነ ከሌላ አገር መሬት አንፈልግም፡፡ ጠቅላይ ሚ/ር ኃይለማርያም ደሳለኝ ተጠይቀው ሲመልሱም ሰምቻለሁ፡፡ እኔም ኢትዮጵያ ለሱዳን መሬት ሰጥታለች የሚለውን አጥብቄ እቃወማለሁ፡፡ በተወራው መሰረት አሁን ሱዳን ሁለት ሚሊዮን ስኩዌር ኪሎ ሜትር ሆናለች ማለት ነው፡፡ የሱዳን የውጪ ጉዳይ ፖሊሲ አንዱ አላማ መልካም ጉርብትና ነው፡፡ ያለምንም ጣልቃ ገብነት ከጎረቤቶቻችን ጋር መኖር ነው፡፡ በፊትም ሆነ አሁን አንድ ኢንች መሬት አይደለም ከኢትዮጵያ ከሌሎች ጎረቤቶቻችንም አንፈልግም፡፡ ሱዳን የኢትዮጵያን መሬት ፈላጊ አይደለችም፡፡ የረጅም ጊዜ የፖለቲካ ስትራቴጂያችን ከድንበር ባሻገር ማሰብ ነው፡፡ ሁለቱን ህዝቦች ያለምንም የድንበር ልዩነት አንድ ማድረግ ነው። ምንም ነገር በሌለበት ሁኔታ ላይ ይህን የሚናገሩ የሁለቱ አገሮች ግንኙነት ያላስደሰታቸው ናቸው፡፡ በጋራ እንሰራለን ያልነው ስራ ስለማያስደስታቸው ነው፡፡ ይህንን ንግግር ኢትዮጵያዊያንም ሆኑ ሱዳናዊያን ትክክል ነው ብለው እንዳይቀበሉ፡፡
በአሁኑ ወቅት የናይል ጉዳይ ዋና አጀንዳ ሆኗል። ካርቱም ነጩ ናይል እና አባይ የሚገናኙባት ቦታ ነች። ምን ትርጉም አለው?
ሁለቱ የሚገናኙበት ቦታ ላይ ብዙ ማለት ይቻላል። ለኔ ሁለቱ ናይሎች የሚገናኙባት ቦታ የሱዳንን አንድነት ታሳየኛለች፡፡ የሱዳንን ህዝብ ይወክላል፡፡ ረጅም መንገድ ተጉዘው ብዙ ጎሳዎችን አልፈው ካርቱም ላይ አንድ ይሆናሉ፡፡ በቅርቡም የተካሄደው የሱዳን ስብሰባ የሱዳንን አንድነት የሚያሳይ ነው፡፡ ሌላው የተፋሰሱ አገሮች አንድነት መገለጫም ነው፡፡ አባይ ከኢትዮጵያ ተነስቶ ብዙ ቦታዎችንና  ህዝቦችን አልፎ ካርቱም ይመጣል። ነጩ ናይልም ከመነሻው ብዙ ኪሎሜትሮችን አቋርጦ፣ብዙ ህዝቦችን አልፎ ካርቱም ይመጣና ይገናኛሉ፡፡ በቅርቡ የናይል ቤዚን ኢኒሽየቲቭ ስብሰባ ላይ ህፃናት “አባይ አባይ” እያሉ ሲዘፍኑ ስሰማ ልቤን በጣም ነካኝ፡፡ የዚያ ዘፈን ትርጉም ብዙ ነው። ሁለቱ ናይሎች ካርቱም ላይ ሲቀላቀሉ ለዘመናት ኖረዋል፡፡ እኛ አሁን ለማድረግ የምንሞክረው ያንን ነው፡፡ እኛ ወረቀት ላይ የናይል ተፋሰስ ስምምነት፣ የምስራቅ ናይል ትብብር የመሳሰሉትን እንላለን። ሁለቱ ናይሎች ግን ካርቱም ላይ ተዋህደው ለዘመናት ፈሰዋል፡፡ አሁንም ይፈሳሉ፡፡ እንዲያውም ይህ የተፈጥሮ ውህደት ያነቃን ይመስለኛል፡፡ እዚህና እዚያ ከምትጨቃጨቁ ለምን  አብራችሁ አትጠጡም የሚል ይመስለኛል፡፡
በታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ላይ የሱዳን አቋም ምንድን ነው ?
አታውቂውም?
ከእርስዎ ልስማው----
በመጀመሪያ የግድቡን ጠቀሜታ እንድናውቅ ላደረጉን ለቀድሞው ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ ምስጋና ይግባ፡፡ ከዛ በኋላ ሶስቱ አገሮች ባቋቋሙት ኮሚቴ ውስጥ በመሳተፋችን ግድቡ ኢትዮጵያ ላይ ቢሠራም ተጠቃሚዎቹ ግብጽ እና ሱዳን መሆናቸውን አውቀናል፡፡ ይህ ለአለምም ይጠቅማል። የግድቡ ፍሬ የሚታወቀው ከኢትዮጵያ ውጪ ላለነው ጭምር ነው፡፡ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት፣ ግድቡ ኬፕታውን እና መካከለኛው ምስራቅ ድረስ ተጠቃሚ ያደርጋል፡፡ ይህ በግድቡ እንድንተማመን አድርጐናል፡፡  ግድቡ እውን እስኪሆን ድረስ ድጋፋችንን እንቀጥላለን፡፡
ለግድቡ ከግንባታ ጋር የተያያዙ ተሽከርካሪዎች ድጋፍ እንዳረጋችሁ ይነገራል፡፡ እውነት ነው?
  እሱን ፈልጊና ድረሽበት፣ እኛ ግን ድጋፋችንን እንቀጥላለን፡፡ ድጋፋችንን ከመጀመሪያውም ገልፀናል፡፡
የቅኝ ግዛት ውሎቹን  ሱዳን በአሁኑ ወቅት  እንዴት ታያቸዋለች?
የውሎቹ ፈራሚዎች ነን፡፡ የ1929 በቅኝ ግዛት ዘመን፣የ1959ኙን ከነፃነት በኋላ ፈርመናል፡፡ በነዚህ ውሎች አሁንም እንገዛለን፡፡ ነገር ግን አሁን አዲሱን የናይል ቤዚን ስምምነት ለመቀላቀል እያሰብን ነው፡፡
የ1929 እና 1959 የቅኝ ግዛት ውሎችን አብዛኞቹ የተፋሰሱ አገሮች በኢንቴቤ ስምምነት ተክተውታል እኮ?
እሱን ነው የምልሽ፡፡ ለመፈረም እያሰብንበት ነው፡፡
ከኢትዮጵያ የምታገኙት የኃይል አቅርቦት እንዴት ነው?
አንደኛ ይህ ፕሮጀክት የአፍሪካ ህብረት ስትራቴጂ እቅድ አገሮችን በኤሌክትሪክ ኃይል ማስተሳሰር የሚለውን የሚተገብር ነው፡፡ በሁለቱ አገሮች ግንኙነት ላይም ጥሩ ነገር የጨመረ ነው። ሁለቱ አገሮች ከተፈራረሟቸውና ከተገበሯቸው ፕሮጀክቶች በማሳያነት የሚቀመጥ ነው፡፡ ወደ ጥያቄሽ ስመጣ የኃይል መቆራረጥ ያለ ቢሆንም አንድ መቶ ሜጋ ዋት እየተጠቀምን ነው፡፡
አቢዬ የሚገኘው የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ ኃይል ቆይታን እንዴት ይገመግሙታል?
በመጀመሪያ በተልዕኮ ላይ እያሉ ህይወታቸውን ላጡ አባላት ቤተሰቦች መፅናናትን እንመኛለን። ይህ መስዋዕትነት በሱዳናዊያን ዘንድ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ነው፡፡ አቢዬ ሄጄ አይቻቸዋለሁ፣ የሚጠበቅባቸውን በአግባቡ እየተወጡ ነው፡፡ ሁለት ቀን አብሬያቸው ነበርኩ፡፡ አንዳንድ መኮንኖችን አነጋግሬያለሁ፡፡ የሱዳን ህዝብ እነሱን በመምረጡ ፀፀት እንዳይሰማው ያደረጉ ናቸው፡፡

     በአዲስ አበባ ወጣቶች ፎረም እና በማኅበረ ወይንዬ አቡነ ተክለሃይማኖት አስተባባሪነት ግብረ  ሰዶማዊነትን የሚቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ሚያዚያ 18 በአዲስ አበባ የሚካሄድ ሲሆን በዛሬው እለትም በግብረ ሰዶም አስከፊነት ላይ ውይይት ይደረጋል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህል አዳራሽ ለግማሽ ቀን በሚካሄደው ህዝባዊ ውይይት ላይ የመንግስት ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣ ጋዜጠኞች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የሃይማኖት ተቋማትና ሌሎች የህብረተሰቡ ክፍሎች የሚሳተፉ ሲሆን የተለያዩ ባለሙያዎች ለውይይት መነሻ የሚሆኑ በግብረ-ሰዶም አፀያፊነት ላይ የሚያጠነጥኑ ፅሁፎች እንደሚያቀርቡ የመድረክ አስተባባሪ ኮሚቴው ገልጿል፡፡ ከፍተኛ የባህል ጥናት ባለሙያ የሆኑት ወ/ሮ አዳነች ካሣ፣ በግብረ ሰዶም ምንነት እና በመጤ ባህሎች ተፅዕኖ ዙሪያ ጥናታዊ ጽሑፍ እንደሚያቀርቡ የተገለፀ ሲሆን የህክምና ባለሙያው ዶ/ር ስዩም አንቶንዮስ በበኩላቸው፤ ድርጊቱ በጤና ረገድ የሚያስከትለውን መዘዝ ያስገነዝባሉ ተብሏል።
ቅዳሜ ሚያዚያ 18 ቀን 2006 ዓ.ም እንዲካሄድ ከአስተዳደሩ እውቅና ያገኘው የፀረ-ግብረ ሰዶማዊነት ሰላማዊ ሰልፍ፣ ከጠዋቱ 2፡00 ሰዓት እስከ ረፋዱ 5፡00 ሰዓት መነሻውን ተክለሃይማኖት አደባባይ አድርጎ፣ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል በኩል በማቋረጥ ማጠቃለያውን ኢትዮ-ኩባ ወዳጅነት አደባባይ ላይ የሚያደርግ ሲሆን የግብረ-ሰዶምን አስከፊነት የሚያቀነቅኑና ግንዛቤ የሚያስጨብጡ መፈክሮች እንደሚስተጋቡ ታውቋል፡፡ በሰልፉ ላይ መንግስት በግብረ-ሰዶማዊነት ላይ የማያወላዳ እርምጃ እንዲወስድ ይጠየቃል ብለዋል - የተቃውሞ ሰልፍ አዘጋጆቹ፡፡
በቅርቡ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ ለግብረ-ሰዶማዊነት ይቅርታ በማያሰጠው የይቅርታ አዋጁ ላይ ተወያይቶ፣ለተጨማሪ ውይይትና የማጠናከሪያ ሃሳብ ለቋሚ ኮሚቴው የመራ ሲሆን ረቂቁ እንደገና በተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ እንደሚፀድቅ ይጠበቃል፡፡ ኡጋንዳ ግብረ-ሰዶማዊነትን የሚከላከልና በድርጊቱ የተሳተፉትን በሞት የሚያስቀጣ ህግ በቅርቡ ያፀደቀች ሲሆን በርካታ ተጠርጣሪዎችም እየታደኑ እንደሆነ ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡
አንዳንድ ወገኖች ህጉን በመቃወም ለተለያዩ ለጋሽ ሃገራት አቤቱታቸውን እያሰሙ ሲሆን በቅርቡም አንዲት የግብረ-ሰዶማዊያኑ መብት ተከራካሪ ወደ ጀርመን አቅንታ፣ የጀርመን መንግስት ለኡጋንዳ መንግስት የሚሰጠውን እርዳታ እንዲቀንስ በመጠየቅ፣ “ሃገሬ ብመለስ በቀጥታ የስቅላት ፍርድ ተግባራዊ ሊደረግብኝ ይችላል” በሚል ጥገኝነት እንደጠየቀች ተዘግቧል፡፡


Published in ዜና

ሶስት ሰዎች ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸው በአዲስ አበባ የተለያዩ ሆስፒታሎች ገብተዋል
“ረብሻውን ያነሱት ህዝብን የማይወክሉ ወሮበሎች ናቸው”      የከተማው ኮሙዩኒኬሽን)

“ባህርዳር በተካሄደው የስፖርት ውድድር ላይ የኦሮሞ ተወላጆች ላይ አድልዎ ተፈጽሟል” በማለት የተቧደኑ ወጣቶች፣ ባለፈው ሐሙስ የሱሉልታ ከተማ ነዋሪ የሆኑ በርካታ የአማራ ተወላጆች ላይ ድብደባ ፈፀሙ፡፡
በድብደባ በርካታ ሰዎች ከመጐዳታቸውም በተጨማሪ፤ ቤት ንብረት ላይም ጥፋት እንደደረሰ የተናገሩት ጉዳት የደረሰባቸው ግለሰቦች ጉዳዩን ሕገወጥ ነው ሲሉ አውግዘውታል፡፡ የከተማዋ ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት ሃላፊ፤ የስፖርት ውድድርን ሰበብ በማድረግ ረብሻ የቀሰቀሱ ሰዎች ህዝብን የማይወክሉ ወሮበሎች ናቸው ብለዋል፡፡
ረብሻውን ቀስቅሰዋል ተብለው ከተጠረጠሩት ውስጥ አራቱን በቁጥጥር ስር ማዋል እንደተቻለም ገልፀዋል ሃላፊው፡፡
“የቤቴ በርና መስኮት እንዳልነበር ሆኗል፤ አጥር ተገነጣጥሏል፤ መስኮቶች ዱቄት ሆነዋል”  ያሉት አንድ የከተማዋ የረጅም ጊዜ ነዋሪ፤ ከ30 በላይ ቤቶች ጉዳት እንደደረሰባቸው ተናግረዋል፡፡   የስድስት ልጆች እናት እንደሆኑ የገለፁልን ሌላዋ ነዋሪ፤ በቤታቸውና በንብረታቸው ላይ አደጋ መድረሱን ጠቅሰው፤ እንደሌሎች ሰዎች ከፍተኛ የአካል ጉዳት ባያጋጥማቸውም በእጃቸው ላይ በደረሰባቸው ጉዳት በከተማዋ አንድ ክሊኒክ ህክምና እንደተደረገላቸው ተናግረዋል፡፡
“ይህ ህዝቡ በሰላም አብሮ እንዳይኖርና እንዳይግባባ ሆን ተብሎ የሚጫር የነገር እሳት ነው” ያሉት የ56 አመት አዛውንት በበኩላቸው፤ መንግስት መፍትሔ ከላበጀለት በቀር በአሁኑ ወቅት ከየአቅጣጫው የምንሰማው በዘር ተቧድኖ ግጭት የመፍጠር ጉዳይ አስጊ ነው ብለዋል፡፡
የከተማው አስተዳደር ኮሙዩኒኬሽን ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ መሳይ ከበደ፤ ከከተማ አስተዳደር በደረሳቸው ሪፖርት ተዘዋውረው እንደተመለከቱ ገልፀው፣ የተወራውን ያህል ባይሆንም የስምንት ቤቶች የበርና የመስኮት መስታወቶች ተሰባብረዋል፤ የቆርቆሮ አጥሮች ተገነጣጥለዋል ብለዋል፡፡  ሰዎች አራት እንደተጐዱና የሶስቱ ሰዎች ጉዳት ከፍተኛ ስለሆነ በአዲስ አበባ የተለያዩ ሆስፒታሎች ውስጥ በክህምና ላይ መሆናቸውን አቶ መሳይ ጠቅሰው፤ አንዲት እናት በእጃቸው ላይ መጠነኛ ጉዳት ደርሶባቸው በከተማው ጤና ጣቢያ ታክመው ተመልሰዋል ብለዋል፡፡
“የረብሻው መንስኤ በቅርቡ ባህርዳር የተካሄደው የመላው ኢትዮጵያ ጫዋታዎች ውድድር ላይ በኦሮሞ ተወላጆች ላይ አድልዎና ተፅእኖ ተደርጓል የሚል ሰበብ ነው” ብለዋል አቶ መሳይ፡፡
“በረብሻው ዙሪያ ህዝቡንና የከተማ ነዋሪውን በመሰብሰብ ረብሻውን ያስነሱት ሰዎች ህዝብን የማይወክሉ እና ህዝብን ለማጋጨት ፍላጎት ያላቸው የተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊዎች መሆናቸውን  ተወያተናል” ያሉት የኮሚዩኒኬሽን ኃላፊው፣ ህዝቡ እንዲህ ዓይነት ቡድኖችም ሆኑ ግለሰቦችን አሳልፎ እንዲሰጥ ተግባብተናል ብለዋል፡፡ ረብሻው ወዲያውኑ በፖሊሶችና ከጫንጮ በመጡ የፀጥታ ኃይሎች መቆሙን ተናግረዋል - ሃላፊው፡፡

Published in ዜና

በአዲስ አበባ ወጣቶች ፎረም እና በማኅበረ ወይንዬ አቡነ ተክለሃይማኖት አስተባባሪነት ግብረ  ሰዶማዊነትን የሚቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ሚያዚያ 18 በአዲስ አበባ የሚካሄድ ሲሆን በዛሬው እለትም በግብረ ሰዶም አስከፊነት ላይ ውይይት ይደረጋል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህል አዳራሽ ለግማሽ ቀን በሚካሄደው ህዝባዊ ውይይት ላይ የመንግስት ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣ ጋዜጠኞች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የሃይማኖት ተቋማትና ሌሎች የህብረተሰቡ ክፍሎች የሚሳተፉ ሲሆን የተለያዩ ባለሙያዎች ለውይይት መነሻ የሚሆኑ በግብረ-ሰዶም አፀያፊነት ላይ የሚያጠነጥኑ ፅሁፎች እንደሚያቀርቡ የመድረክ አስተባባሪ ኮሚቴው ገልጿል፡፡ ከፍተኛ የባህል ጥናት ባለሙያ የሆኑት ወ/ሮ አዳነች ካሣ፣ በግብረ ሰዶም ምንነት እና በመጤ ባህሎች ተፅዕኖ ዙሪያ ጥናታዊ ጽሑፍ እንደሚያቀርቡ የተገለፀ ሲሆን የህክምና ባለሙያው ዶ/ር ስዩም አንቶንዮስ በበኩላቸው፤ ድርጊቱ በጤና ረገድ የሚያስከትለውን መዘዝ ያስገነዝባሉ ተብሏል።
ቅዳሜ ሚያዚያ 18 ቀን 2006 ዓ.ም እንዲካሄድ ከአስተዳደሩ እውቅና ያገኘው የፀረ-ግብረ ሰዶማዊነት ሰላማዊ ሰልፍ፣ ከጠዋቱ 2፡00 ሰዓት እስከ ረፋዱ 5፡00 ሰዓት መነሻውን ተክለሃይማኖት አደባባይ አድርጎ፣ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል በኩል በማቋረጥ ማጠቃለያውን ኢትዮ-ኩባ ወዳጅነት አደባባይ ላይ የሚያደርግ ሲሆን የግብረ-ሰዶምን አስከፊነት የሚያቀነቅኑና ግንዛቤ የሚያስጨብጡ መፈክሮች እንደሚስተጋቡ ታውቋል፡፡ በሰልፉ ላይ መንግስት በግብረ-ሰዶማዊነት ላይ የማያወላዳ እርምጃ እንዲወስድ ይጠየቃል ብለዋል - የተቃውሞ ሰልፍ አዘጋጆቹ፡፡
በቅርቡ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ ለግብረ-ሰዶማዊነት ይቅርታ በማያሰጠው የይቅርታ አዋጁ ላይ ተወያይቶ፣ለተጨማሪ ውይይትና የማጠናከሪያ ሃሳብ ለቋሚ ኮሚቴው የመራ ሲሆን ረቂቁ እንደገና በተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ እንደሚፀድቅ ይጠበቃል፡፡ ኡጋንዳ ግብረ-ሰዶማዊነትን የሚከላከልና በድርጊቱ የተሳተፉትን በሞት የሚያስቀጣ ህግ በቅርቡ ያፀደቀች ሲሆን በርካታ ተጠርጣሪዎችም እየታደኑ እንደሆነ ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡
አንዳንድ ወገኖች ህጉን በመቃወም ለተለያዩ ለጋሽ ሃገራት አቤቱታቸውን እያሰሙ ሲሆን በቅርቡም አንዲት የግብረ-ሰዶማዊያኑ መብት ተከራካሪ ወደ ጀርመን አቅንታ፣ የጀርመን መንግስት ለኡጋንዳ መንግስት የሚሰጠውን እርዳታ እንዲቀንስ በመጠየቅ፣ “ሃገሬ ብመለስ በቀጥታ የስቅላት ፍርድ ተግባራዊ ሊደረግብኝ ይችላል” በሚል ጥገኝነት እንደጠየቀች ተዘግቧል፡፡


Published in ዜና

‘ዘ ናይንቲ ናይን ሲሪየስ’ የተሰኘው የአይዳ ሙሉነህ ስራ

የታዋቂዋ ኢትዮጵያዊት ፎቶግራፈር አይዳ ሙሉነህ እና የኢትዮ-አሜሪካዊቷ ሰዓሊ ጁሊ ምህረቱ የስነ-ጥበብ ስራዎች፣ በፍራንክፈርት የሞደርን አርት ሙዚየም (MMK) ውስጥ  በተከፈተ አለም አቀፍ ኤግዚቢሽን በመታየት ላይ እንደሚገኙ ታዲያስ ከኒውዮርክ ዘገበ፡፡
ታዋቂ አፍሪካውያን ዘመናዊ አርቲስቶች ስራዎቻቸውን ያቀረቡበትና ጣሊያናዊው የ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን  ገጣሚ ዳንቴ በጻፈው ‘ዘ ዲቫይን ኮሜዲ’ የተሰኘ የግጥም ስራ የተሰየመው ‘ሄቨን፣ ሄል፣ ፑርጋቶሪ ሪቪዚትድ ባይ ኮንቴምፖራሪ አፍሪካን አርቲስትስ’ የተባለው አለም አቀፍ የስነ-ጥበብ ኤግዚቢሽን፣ እስከ መጪው ሃምሌ አጋማሽ ድረስ ለተመልካች ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡
በታዋቂው የስነ-ጥበብ አጋፋሪ ሲሞን ጃሚ እና በሞደርን አርት ሙዚየም ትብብር በተዘጋጀው በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ የቀረቡት ስራዎች፣ በቀጣይም በተለያዩ የአለም አገራት በሚገኙ አራት ቦታዎች ለእይታ እንደሚበቁ ተነግሯል፡፡
ከዚህ ቀደሞቹ  ከአፍሪካ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ኤግዚቢሽኖች በተለየ የአፍሪካ ስነ-ጥበብ፣ የድህረ ቅኝ-ግዛት ጉዳዮችን ማንጸባረቅ ብቻ ሳይሆን ውበትን አጉልቶ በማሳየት ጭምር ጥቅም ላይ ሊውሉ ይገባል በሚል እምነት የዘንድሮውን ኤግዚቢሽን እንዳዘጋጀ፣ ሞደርን አርት ሙዚየም አመልክቷል፡፡
‘ዘ ናይንቲ ናይን ሲሪየስ’  የተሰኘውን ጨምሮ የተለያዩ ስራዎቿን በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ ለእይታ ያበቃችው አይዳ ሙሉነህ፣ ከሃዋርድ ዩኒቨርሲቲ በፊልም፣ በሬዲዮና በቴሌቪዥን ሙያ የመጀመሪያ ዲግሪዋን ያገኘች ሲሆን፣ ስራዎቿን በተለያዩ ታላላቅ ኤግዚቢሽኖች ላይ ከማቅረብ ባለፈ፣ በርካታ አለማቀፍ ሽልማቶችን ለማግኘት የቻለች የፎቶግራፍ ባለሙያ ናት፡፡  
በአሁኑ ወቅት፣ ‘ደስታ ፎር አፍሪካ’ (DFA Creative Consulting plc.) የተባለና ትኩረቱን የፈጠራ ሥራዎች ላይ በማድረግ፤ ለአገር ውስጥና ለዓለም አቀፍ ገበያ የሚሆኑ የፈጠራ ሃሳቦችን የማማከር፣ ደረጃቸውን የጠበቁ ፎቶግራፎችን የማንሳትና ባህላዊ ዝግጅቶችን የማቀድ አገልግሎቶችን የሚሰጥ ኩባንያ በማቋቋም፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የተለያዩ ስራዎችን በማከናወን ላይ ትገኛለች፡፡
የታላላቅ ኢትዮጵያውያን ሴቶችን ታሪክ በሚተርከውና በቅርቡ ለህትመት እንደሚበቃ በሚጠበቀው ‘ተምሳሌት’ የተሰኘ መጽሃፍ ውስጥ የተካተቱት በርካታ ፎቶግራፎችም በአይዳ የተነሱ ናቸው፡፡
ነዋሪነቷ በኒውዮርክ የሆነው ኢትዮ-አሜሪካዊቷ ሰዓሊ ጁሊ ምህረቱም፣ በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የስነጥበብ ትምህርቷን የተከታተለች በአለማቀፍ ደረጃ የምትጠቀስ ሰዓሊ ናት፡፡ የተለያዩ አለማቀፍ ሽልማቶችን የተቀበለች ሲሆን  የስዕል ስራዎቿም በከፍተኛ ዋጋ ተሸጠውላታል፡፡ ከእነዚህም መካከል፣ የዛሬ አራት ዓመት በታዋቂው አጫራች ድርጅት ሱዝቤይ አማካይነት፣ 1 ሚሊዮን 22 ሺህ  ዶላር (20 ሚሊዮን ብር ገደማ) የተሸጠላት ርዕስ አልባ ስዕሏ  ይጠቀሳል፡፡

Published in ዜና

ማኅበረ ቅዱሳን÷ በየመድረኩ ከሚሰማው የአክራሪነት ፍረጃና ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ እንቅስቃሴ ጋራ በተያያዘ የገጠሙትን የስም ማጥፋትና የማኅበሩን አገልግሎት የማሰናከል ወቅታዊ ተግዳሮቶች፣ ተቀራርቦ በግልጽ በመመካከርና በጸሎት መፍትሔ ለማስገኘት ሲያደርግ የቆየውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገለጸ፡፡
የማኅበሩ የሥራ አመራር ጉባኤ ከመጋቢት 27 - 28 ቀን 2006 ዓ.ም በአቡነ ጎርጎሬዎስ ት/ቤት አዳራሽ ባካሔደውና ከ46 የሀገር ውስጥና የውጭ ማእከላት የተውጣጡ 160 ያህል አመራሮች በተሳተፉበት የመንፈቅ ዓመት መደበኛ ስብሰባ በወቅታዊ ኹኔታዎች ላይ ባደረገው ግምገማ፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማዊ ህልውናና በማኅበሩ አገልግሎት ቀጣይነት ላይ ተጋርጧል ያላቸውን ወቅታዊ ተግዳሮቶች በዝርዝር በማንሣት የመፍትሔ አቅጣጫ ማስቀመጡ ተጠቁሟል፡፡
የሥራ አመራር ጉባኤው ለማኅበሩ አስፈጻሚ አካል ባስቀመጠው የመፍትሔ አቅጣጫ፣ ማኅበሩ በቅ/ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው መተዳደርያ ደንብ መሠረት ትውልዳዊ ተልእኮውን ለአባቶች በመታዘዝና በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን በመወሰን የመፈጸም አሠራሩና ፍላጎቱ እንደጸና መኾኑንና ለወቅታዊ ተግዳሮቶቹ በግልጽ ተቀራርቦ ከመመካከርና ከጸሎት ውጭ በሌላ መንገድ የሚመጣ መፍትሔ ይኖራል ብሎ እንደማያምን አስታውቋል፡፡
የሥራ አመራር ጉባኤው በተዛባ አመለካከትና በሐሰተኛ ክሥ የቤተ ክርስቲያኒቱን አባቶችና የመንግሥት አካላትን ግራ በማጋባትና በማሳሳት የማኅበሩን አገልግሎት ማስተጓጎል ዋነኛ አጀንዳ አድርገዋል ባላቸው ግለሰባዊና ቡድናዊ ቅስቀሳዎች ላይ በትኩረት መወያቱ ተነግሯል፡፡
መንግሥት ከሚያካሒደው የፀረ አክራሪነት ትግልና ከቤተ ክርስቲያኒቷ የአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ አፈጻጸም ጋራ በማያያዝ የሚሰነዘሩበትን የስም ማጥፋት ዘመቻዎችና መሠረተ ቢስ ክሦች ከአባቶች፣ ከአስተዳደር ሓላፊዎች፣ ከሰንበት ት/ቤቶች፣ ከመንፈሳውያን ማኅበራትና ከመላው ምእመናን ጋራ ተቀራርቦ በመረዳዳትና በጸሎት ፍትሐ እግዚአብሔርን በመጠየቅ የመፍታት የወትሮ ጥረቱ ተጠናክሮ የሚቀጥልበትን አቅጣጫ ማስቀመጡንም ምንጮች ገልጸዋል፡፡
የማኅበሩ ዓላማና ፍላጎት ከቤተ ክርስቲያኒቱ ሐዋርያዊ ተልእኮ የሚነሣና ጥቅሙም ለቤተ ክርስቲያኒቱ በመኾኑ ከቤተ ክርስቲያኒቱና ከሀገሪቱ ህልውና የሚቀድም የተለየ የማኅበር (ቡድናዊ) ዓላማና ጥቅም እንደሌለም የሥራ አመራር ጉባኤው ያወጣው ውሳኔ ያመለክታል፡፡
አባላቱንና ተቋማዊ አሠራሩን በተመለከተ በማስረጃ ተደግፈው የሚቀርቡለትን ችግሮች ከመተዳደርያ ደንቡና ከውስጣዊ አሠራሩ አኳያ ያለማመንታት ለማረም ምንጊዜም ዝግጁ እንደኾነ የመከረው የሥራ አመራር ጉባኤው፥ ቤተ ክርስቲያናቸውን ከመከባከብ ባሻገር ለሀገራቸው ልማታዊ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ለማበርከት የሚበቃ አቅምና ሥነ ምግባር እንዳላቸው የሚያምንባቸውን ከ30ሺሕ መደበኛና ከግማሽ ሚልዮን በላይ ደጋፊ አባላት ያቀፈውን ይህን መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር በማበረታታት የድርሻውን እንዲወጣ ከማድረግ ይልቅ፣ በተለያዩ ክሦችና ውንጀላዎች ለማሸማቀቅ ያለዕረፍት የሚደረገው ሐሰተኛ ቅስቀሳና የክሥ ዘመቻ አግባብነት እንደሌለው ውጤትም እንደማያመጣ አስታውቋል፡፡    

Published in ዜና

“ተጨባጩንና እውነተኛውን ነገር በጠበቃዬ በኩል ለፍ/ቤት አቅርቤያለሁ”

በተለይ “ገመና” በተሰኘው ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ ላይ የዶ/ር ምስክርን ገፀ-ባህሪ ተላብሶ በመጫወት እውቅናን ያተረፈው አርቲስት ዳንኤል ተገኝ፤ የ600 ሺህ ብር ክስ የተመሠረተበት ሲሆን አርቲስቱ ለተከሰሰበት ጉዳይ ምላሽ እንዲሰጥ ፍ/ቤቱ ለትላንትና ትዕዛዝ አስተላልፎ ነበር፡፡
ክሱ መመስረቱን ያልካደው አርቲስት ዳንኤል፤ ሆኖም “ክሱ መሰረተ ቢስና ከእውነት የራቀ መሆኑን በመግለፅ ተጨባጩን እውነታ አስፍሬ በጠበቆቼ በኩል ለፍ/ቤት ምላሽ ሰጥቻለሁ” ብሏል - ጉዳዩ በፍ/ቤት የተያዘ በመሆኑ ከዚህ በላይ ለመናገር እንደማይፈልግ በመግለፅ፡፡
አርቲስት ዳንኤልና ወ/ሮ ቤተልሄም አበበ፤ “ፋየር ፕሩቭ” የተሰኘ የእንግሊዝኛ ፊልም ወደ አማርኛ በመመለስ አብረው ለመስራት ውል ተፈራርመው የነበረ ሲሆን “አርቲስቱ በገባው ውል መሰረት ስራውንም አልሰራም ብሬንም አልመለሰም” በማለት ወ/ሮ ቤተልሄም የ662 ሺህ 120 ብር ክስ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 6ኛ ፍትሀ ብሔር ቢፒአር ችሎት መመስረታቸው  ታውቋል፡፡
አርቲስት ዳንኤል “ፋየር ፕሩቭ” የተሰኘ የእንግሊዝኛ ፊልም ወደ አማርኛ በመመለስ ስምንት ያህል ትዕይንቶችን ከቀረፀ በኋላ አቋርጦ “የሴም ወርቅ” የተሰኘ ሌላ ፊልም መስራት የጀመረ ሲሆን በዚህ ወቅት ነበር ወ/ሮ ቤተልሔም እሱ የጀመረውን ፊልም “አብረን  እንስራ” የሚል ጥያቄ ያቀረቡለት- አርቲስቱ በቅርቡ ለአዲስ አድማስ እንደተናገረው፡፡
አርቲስቱ የጀመረውን “ፋየር ፕሩቭ” የተሰኘ ፊልም ከወ/ሮ ቤተልሔም ጋር አብረው ለመስራት ተስማምተው ከተዋዋሉ በኋላ ወደ ሥራው የገቡ ቢሆንም በኋላ ላይ “ወ/ሮዋ የስነ ምግባር ጉድለት ስላለባቸው አብሬያቸው መስራት አልቻልኩም” በሚል ዳንኤል ስራውን ያቆመ ሲሆን ወ/ሮ ቤተልሄም በበኩላቸው፤አርቲስቱ በውሉ መሰረት ፊልሙን በጊዜ ሰርቶ ባለማስረከቡ ብሩን እንዲመልስ መጠየቃቸውንና እሱም ብር አልወሰድኩም በማለቱ ግጭቱ እንደተካረረ መዘገቡ  ይታወሳል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ የኢትዮፒካሊንክ የሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጆች ከወ/ሮ ቤተልሄም ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ፣“የስም ማጥፋት ዘመቻ አካሂደውብኛል” ያለው አርቲስቱ፤በግለሰቧና በአዘጋጆቹ ላይ ክስ መመስረቱን ታህሳስ 12 ቀን 2006 ዓ.ም ለንባብ በበቃው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ተናግሯል፡፡
ወ/ሮ ቤተልሔም የካቲት 7 ቀን 2006 ዓ.ም በአርቲስት ዳንኤል ላይ የ662ሺህ 120 ብር ክስ መመስረታቸውን የጠቆሙት ምንጮቻችን፤ ከሳሿ የቼክ ቁጥሮችን በማስረጃነት አያይዘው ለፍ/ቤቱ እንዳቀረቡ ገልፀዋል፡፡ ምንጮች እንደሚሉት፤ ወ/ሮ ቤተልሄም አበበ ወደ ክስ ለመሄድ የተገደዱት ለፊልሙ መስሪያ ብለው ለአርቲስቱ የሰጡትን ገንዘብ እንዲመልስ ሲጠይቁት “ብር አልወሰድኩም” በማለቱ ነው፡፡ ፍ/ቤቱ አርቲስት ዳንኤል ለቀረበበት ክስ በትላንትናው እለት ምላሽ እንዲሰጥ  ትዕዛዝ አስተላልፎ የነበረ ሲሆን አርቲስቱም ምላሹን በጠበቆቹ በኩል ለፍ/ቤት ማስገባቱን ገልጿል። ፍ/ቤቱ ግራ ቀኙን ተመልክቶ ብይን ለመስጠት ለሚያዚያ 12 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡  

Published in ዜና