ጥራት የሚለካው በደንበኛ እርካታ ነው
ዶ/ር ኢ/ር ዳንኤል ቅጣው በ1972 ዓ.ም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በሜካኒካል ኢንጅነሪንግ በከፍተኛ ማዕረግ ተመረቁ።
በተማሩበት ዩኒቨርሲቲ በረዳት መምህርነትና በመምህርነት ለሁለት ዓመት ከሠሩ በኋላ፣ ለሁለተኛ ዲግሪያቸው ጣሊያን ሄዱ። በጣሊያን ፖሊቴክኒኮ ዲ ቶሪኖ እና ፖሊቲክኒኮ ዲ ሚላኖ የሚባሉ ሁለት ከፍተኛ ዩኑቨርሲቲዎች አሉ። ዶ/ር ኢ/ር ዳንኤል በፖሊቴክኒኮ ዲ ቶሪኖ ትምህርታቸውን ተከታትለው ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በኢንዱስትሪያል ኢንጅነሪንግ ተመርቀው በ1977 ዓ.ም ወደ አገራቸው ተመልሰው በአ.አ.ዩ ሜካኒካል ኢንጅነሪንግ ሲያስተምሩ ቆዩ።
በ1988 ዓ.ም ለሦስተኛ ዲግሪያቸው ተመልሰው ወደ ጣሊያን ሄዱ። እዚያም ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በተማሩበት በፖሊቴክኒኮ ዲ ቶሪኖ ዩኒቨርሲቲ የዶክትሬት ዲግሩ ትምህርታቸውን ተከታትለው በ1992 ዓ.ም በኢንዱስትሪያል ኢንጅነሪንግ በዶክትሬት ዲግሪ ተመረቁ፡ ከዚያ እንደተመለሱ እስካሁን ድረስ በአ.አ.ዩ በስኩል ኦር ሜካኒካል አንድ ኢንዱስትሩ የትምህርት ክፍል በተባባሪ ፕሮፌሰርነት ማዕረግ በመምህርነት እየሰሩ ነው። የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ መንግሥቱ አበበ ከዶ/ር ኢ/ር ዳንኤል ቅጣው ጋር በጥራትና በምርታማነት ዙሪያ ያደረገውን ቃለ ምልልስ እነሆ!

ጥራት ወይም ኳሊቲ ምንድነው?
ይህ ጥያቄ በጣም አጭር ነገር ግን በጣም በጣም ሰፊ ምላሽ ያለው ሐሳብ ነው። ጥራት ወይም ኳሊቲ የምንለው ሐሳብ፣ እንደቃል ሳይሆን እንደፍልስፍና የሚታይ ነው። የአዕምሮ መለወጥን የሚጠይቅ፣ ደንበኛን ከደንበኛ የሚያያይዝ፣ ከደንበኛ ፍላጐት ጋር የተገናኘ ነው። የጥራት ትርጉም አሰጣጥ፣ በብዙዎች ዘንድ ስህተት ፈጥሯል። አንዳንድ ጊዜ የሚያብለጨልጭ፣ ከፍተኛ ዋጋ ያለው ወይም ለየት ያለ ነገር፣ …”ኳሊቲ ነው” ሲባል እንሰማለን። ኳሊቲ ክራቫት አስሯል፤ ኳሊቲ ልብስ ለብሷል፣ ኳሊቲ ጫማ አድርጓል… ይባላል። እነዚህ ነገሮች፣ ኳሊቲ የሚባለው ጽንሰ ሐሳብ ውስጥ ሊኖሩ ይችላሉ፤ ነገር ግን የኳሊቲ ፅንሰ ሐሳብ ይህ ብቻ አይደለም።
ጥራት ወይም ኳሊቲ በአጭሩ፣ ደንበኛው የሚፈልገውን አገልግሎትም ሆነ ዕቃ ልክ ደንበኛው እንደሚፈልገው ወይም ከሚፈልገው በተሻለ ሁኔታ፣ ደንበኛው በሚፈልገው ጊዜ፣ በሚፈልገው ብዛት፣ ሊገዛ በሚችለው አቅም ማቅረብ ማለት ነው። ለምሳሌ፣ አንድ ሰው “ከአንድ ግመልና ከአንድ ቮልቮ ከባድ መኪና የቱ ነው ጥራት ያለው?” ተብሎ ቢጠየቅ፣ ለጥራት ባለው ግንዛቤ መሠረት “ቮልቮ ነው” ሊል ይችላል። ግን እንደዚያ አይደለም። በረሃ ውስጥ ከሆነ ቮልቮ ሊሄድ አይችልም፤ ስለዚህ እንደተጠቃሚው ወይም እንደደንበኛው ፍላጐት በረሃ ውስጥ ከሆነ ግመል ጥሩና የተሻለ ስለሚሆን ጥራት አለው ማለት ነው። አውራ ጐዳና ላይ ከሆነ ግን ግመል አይደለም የሚያስፈልገው። ጥራት ያለው ቮልቮ ሊሆን ይችላል። ስለዚህ ጥራት፤ የተጠቃሚውን (የደንበኛውን) ፍላጐት፣ ቦታ፣ አቅም፣ አካባቢ… ያገናዘበ ነው ማለት ነው።
ጥራት ማለት ከደንበኛ ጋር የተያያዘ ነው ብለውናል። ስለዚህ ባገራችን የጥራት ትርጉም በኀብረተሰቡ ውስጥ እንዲሰርፅ ልጆቻችንን፣ ከመዋዕለ ሕፃናት ጀምሮ ደንበኛ ማክበርን ልናስተምራቸው ይገባል። ስለጥራት ከተነሳ፣ የደንበኛ መኖር የግድ ነው። አገልግሎትና ቁስ መቀባበል ብቻ፣ ዕቃ መሸጥና ያለመሸጥ፣ በፋብሪካ ውስጥ ጥሩ ዕቃ ማምረት ወይም ያለማምረት ብቻ አይደለም። እርስ በርስ ስንገናኝ ጀምሮ አንዱ የሌላው ደንበኛ ነው። ሕፃናት ዕቃ ሲነጣጠቁ… ዕቃ የሌለው ልጅ፣ ዕቃ ያለው ልጅ ደንበኛ ነው። “እባክህን፣ ይህን ዕቃህን ልጠቀምበት?” ብሎ እንዲጠይቅ ብናስተምረው ወይም ይህን ፍልስፍና እውስጡ ብናሰርፅ ማክበር እየለመደ ያድጋል። ያደጉ አገሮች ከሚታወቁባቸው ዋና ዋና ነገሮች አንዱ ደንበኛን ማክበር ነው።
በአሜሪካ አንድ ሰው ዕቃ ገዝቶ፣ እቤቱ ከደረሰ በኋላ ዕቃው ባይስማማው፣ ወደገዛበት ሱቅ ተመልሶ “አልፈልገውም፣ መልሼዋለሁ” በማለት ገንዘቡን መቀበል ወይም ሌላ የሚፈልገውን ዕቃ ለውጦ መውሰድ ይችላል። ይኼ አሰራር የመጣው ደንበኛውን ከማክበር ነው። የሠራተኞቹን ደሞዝ የሚከፍለውና ለዚያ ድርጅት መኖር ምክንያቱ ደንበኛው ነው።
ወደ አውሮፓ ስንሄድም ደንበኛ ይከበራል፤ የተሸጠ ዕቃ ይመለሳል። ከአሜሪካኖቹ የተለየ አውሮፓውያኑ ያወጡት ሕግ አለ። “ዕቃውን የገዛህበትን ቲኬት መያዝ አለብህ፤ ዓርማው ወይም ታጉ መኖር አለበት” የሚል ነው። ይሄ ስለኳሊቲ ያላቸው ግንዛቤ ከአሜካውያኑ ያነሰ መሆኑን ያሳያል። ወደ እኛ አገር ስንመጣ ደግሞ፣ ጥሩ ባለሱቅ ከሆነ በትላልቅ ፊደሎች “የተሸጠ ዕቃ አይመለስም” የሚል ጽፎ ፊት ለፊት ይለጥፋል። ይኼ ደንበኛን ካለማክበር የሚመነጭ ነው። ጥራት የተመሠረተበትን ያለማወቅና ያለመረዳት የሚያመጣው ችግር ነው። ስለጥራት፣ ስለደንበኛ አያያዝ ማን አስተማረን? ማንም! ብዙ ጊዜ “ደንበኛ ንጉሥ ነው” እየተባለ ሲነገር እንሰማለን። በየሱቁና በየድርጅቱም ተለጥፎ እናያለን። ግን ደንበኛ አይከበርም። ይህ የሚያሳየው፣ ከቃሉ እንጂ ከጽንሰ ሐሳቡ ጋር እንደማንተዋወቅ ነው። ስለዚህ የአመለካከታችን አወቃቀር መለወጥ አለበት፣ የአስተሳሰብና የአመለካከታችንን ውቅር መለወጥ (የፓራዳይም ሺፍት) ያስፈልገናል።
መንገድ ላይ በመኪና ስሄድ በጣም አዝናለሁ። ብዙ ጊዜ መኪኖች እርስበርስ ተዘጋግተው ይቆማሉ። መዘጋጋቱ የሚፈጠረው መንገዶቹ በመጥበባቸው ወይም ተሽከርካሪዎቹ በመብዛታቸው ብቻ አይደለም። እርስበርስ ስለማንከባበር ነው። የመኪና መንገድ ስንጠቀም፣ አንዳችን የሌላችን ደንበኛ ነን። እኔ ከቀኜ ለሚመጣ መኪና ቅድሚያ የመስጠት ኃላፊነትና ግዴታ አለብኝ። ከጐኔ ያለው አሽከርካሪ ደንበኛዬ ነው፤ እኔ ደግሞ የእሱ ደንበኛ ነኝ። ብንከባበር፣ እሱም ይሄዳል፣ እኔም እሄዳለሁ። ጥቁርና ነጭ በተቀባ የእግረኛ ማቋረጫ (ዜብራ) ላይ የእግረኛ መብት አናከብርም። ባለመኪና አይደለን፣ ጉልበተኞች ነን። እንዲያ መሆን የጥራት ፍልስፍናን ግንዛቤያችን ዝቅተኛ ነው ማለት ነው። ዜብራ ላይ ስደርስ መኪናዬን አቁሜ ለእግረኞች  “እለፉ” የሚል ምልክት ስሰጣቸው በጣም ያመሰግኑኛል። የሚፈልጉትን ነገር ስላደረግሁላቸው ደስ ብሏቸው ነው። አላወቁትም እንጂ መብታቸው እኮ ነው። አብዛኞቻችን ግን ጥራትን ከምርት ጋር ብቻ ነው የምናያይዘው…
ጥራት ስንል፣ በፍፁም ከሸቀጥ (ኮሞዲቲ) ጋር ብቻ የተያያዘ  አይደለም። ለምሳሌ አንድ ሐኪም፣ ታካሚ ደንበኞች አሉት። እነሱ በመኖራቸው ነው ሐኪሙ የሚሰራው። ስለዚህ ደንበኞቹን (ታካሚዎቹን) ተንከባክቦ መያዝ አለበት። እዚህ ላይ አንባቢ እንዲረዳኝ የምፈልገው፣ የሐኪሞችን የሥራ መደራረብና ጫና እንዲሁም የቁጥራቸውን ማነስ፣ ግምት ውስጥ ሳላስገባ አይደለም። ግን መሆን የነበረበትን ነው የምናገረው። ችግሬ ምን እንደሆነ ጠይቆ ሳይረዳና ሳይመረምረኝ፣ ገና በሩን እንደገባሁ፣ አቀርቅሮ ወረቀት እየጻፈ፣ “ምንህን ነው ያመመህ?” በማለት ይጠይቀኛል እንጂ እንደሰውና እንደንበኛው አያየኝም፤ አያስተናግደኝም። ይኼ የጥራት ፍልስፍና ማነስ ስለሆነ ሐኪሞች አዕምሮአቸውን (አመለካከታቸውን) መለወጥ አለባቸው። በሌላውም ዘርፍ እንዲሁ ነው።
እኛ አስተማሪዎች፤ ተማሪዎቻችንን እንዴት ነው የምናየው? ተማሪ ባይኖር እኔ‘ኮ ሥራ የለኝም። ምርምር መሥራት እችላለሁ። ነገር ግን የማስተርስና የዶክትሬት ተማሪዎች ከሌሉ እንዴት ምርምር መሥራት እችላለሁ? አልችልም። ተማሪዎቼ የእኔ ኃላፊዎችና ደንበኞች ስለሆኑ ላከብራቸው ይገባል። ይህ ማለት ግን የማይገባቸውን ውጤት መስጠት፣ በማይሆን ሁኔታ ማባባል፣ ትከሻ ላይ አውጥቶ መሸከም ማለት አይደለም። እንደሰው፣ እንደደንበኛ መታየትና መከበር ይገባቸዋል ማለቴ ነው። ይኼ ነው ጥራት ማለት። ጥራት ከደንበኛ ከተለየ ትርጉም የለምውም ማለት ነው፤ ደንበኛ ሳይኖር ስለ ጥራት ማውራት አንችልም።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ እኮ የሚሠራው(የሚኖረው) እኔና ሌሎች ተሳፋሪዎች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ስንሆንለት ነው። ስለዚህ፣ ተሳፋሪውን በሚገባ መንከባከብና ማስተናገድ አለበት። ሲዘገይ፣ “ይቅርታ ዘግይተናል፤ ለዚህ ጥፋታችንም ማካካሻ እናደርጋለን” በማለት የደንበኞቹን ቅሬታ ማስወገድ አለበት። አስተማሪም ሲያረፍድ፤ “ይቅርታ እንዲህ ዓይነት ችግር አጋጥሞኝ ነው” ብሎ ትክክለኛውን ምክንያት በመንገር፣ ተማሪዎቹን ይቅርታ መጠየቅ አለበት። ምክንያቱም አስተማሪውንና ተማሪውን የሚያገናኘው ኮርሱ ወይም ትምህርቱ ነው። ለምሳሌ ነገ ለተማሪዎቼ የጥራት ኮርስ አስተምራለሁ። ኮርሱ፣ ለእኔ ምርቴ ነው። እሱን ነው የምሸጥላቸው። ኮርሱን ካልገዙኝ ወይም “ዳንኤል የተባለው አስተማሪ ሁለተኛ ክፍላችን እንዳይገባ” ብለው ከከለከሉኝ፣ ሥራዬን አጣለሁ ማለት ነው። ስለዚህ ደስ ብሏቸው ኮርሱን እንዲገዙኝ መትጋት አለብኝ። ነገር ግን ዲግሪውን ስለሚፈልጉት በማስፈራራት ወይም “ምን ታመጣላችሁ!” በሚል ስሜት ኮርሱን መስጠት የለብኝም። እንዲህ ያለው አሠራር ከጥራት ፍልስፍና ውጭ ነው።
ለመሆኑ ጥራት በምን ይለካል?
ጥራት በደንበኛው እርካታ ነው የሚለካው። የመንገድ ጥራት፣ የልብስ ጥራት ወይም የምርትና የአገልግሎት ጥራት ስንል ደንበኛው ባዘዘውና በጠየቀው መመሪያ ነው ወይ የተሠራለት? ብለን መፈተሽ እንችላለን። ለምሳሌ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን፣ መንገድ የሚሠሩለትን ኮንትራክተሮች ጋብዞ ያወዳድራል። ደንበኛው የመንገዶች ባለሥልጣን ነው። እኛ ደግሞ ከእኛ በተሰበሰበ ታክስ መንገዱ ስለሚሠራና ተጠቃሚዎች ስለሆንን ተጨማሪ ደንበኞች ነን። ባለሥልጣን መ/ቤቱ እንዲሠራለት የሚፈልገውን ዓይነት መንገድ ዝርዝር መመሪያ (ስፔሲፊኬሽን) ያቀርባል። የሚሠራው መንገድ ሳይበላሽ ለ10 ዓመት የሚያገለግል፣ ወጣ ገባ የሌለው፤ 8፣ 12፣ 14፣ …ሜትር ስፋት ያለው፣ በሁለቱም ጐን ውሃ ወደ ውጭ የሚያፈስ የመንገድ ትከሻ ያለው፣ መንገዱ ተሠርቶ ሲያልቅ፣ ቁልቁለት ወይም መጠምዘዣ መኖሩን የሚጠቁም ምልክት ያለው፣ የጥገናው ወጪ አነስተኛ የሆነ… ብሎ ፍላጐቱን በመግለጽ አወዳድሮ ኮንትራቱን ለአሸናፊው ድርጅት ይሰጣል።
እንግዲህ ጥራት የምንለው ደንበኛው በፈለገው ዝርዝር መመሪያ መሠረት መሠራቱን ነው። አንዳንድ ጊዜ ደንበኛው ፍላጐቱን በትክክል ያስቀምጣል። አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ያሰበውንና የፈለገውን ነገር በትክክል ላይገልጽ ይችላል። ስለዚህ ጥራት ማለት የተገለፀውንና ያልተገለፀውን የደንበኛውን ፍላጐት ጭምር ማርካት ማለት ነው። በዚህ ነው ጥራት የሚለካው።
የጥራት መለኪያና መመዘኛ የሚባሉ አውታሮች (ዳይመንሽኖች) አሉ። ለምሳሌ፣ ይኼ ከዚህኛው ይበልጣል ወይም ይሻላል ለማለት ተመሳሳይ ይዘት ያላቸውን ነገሮች ነው የምናወዳድረው። ፈረስን ከፈረስ እንጂ ከበግ ጋር አናወዳድርም። እንዲህ በምናደርግበት ጊዜ ሲስተሙን ኳሊቲ ዳይመንሽን እንለዋለን። አንደኛው የጥራት መለኪያ ፋንኪሽናሊቲ፣ የምንፈልገውን ነገር ይሠራል ወይ የሚለው ነው። ሁለተኛው ፐርፎርማንስ፣ የመሥራት አቅምና ብቃቱ ነው። ለምሳሌ አንድ የልብስ ስፌት መኪና 8 ሰዓት ይሠራል ከተባለ፣ በተከታታይ ለ8 ሰዓት ያለ አንዳች እክል ይሠራል ወይ? ማለት ነው።
ሌላው ሪያሊቢሊቲ (አስተማማኝነት) ነው። ጥገና አስፈላጊ ነገር ቢሆንም፣ በአዲስነቱ ምን ያህል ጊዜ ሳይበላሽ በአስተማማኝነት ይሠራል? ወይም በመጀመሪያውና በሁለተኛው ጥገና መካከል ባለው ጊዜ በአስተማማኝነት ይሠራል? የሚለው ነው። ሌላው የጥራት መመዘኛ ደግሞ ኮንፎርሚቲ የምንለው ነው። ሌላው ደግሞ ዱረቢሊቲ ነው። ዱረቢሊቲ ስንል ጥንካሬውን ማለታችን ነው። ለረዥም ጊዜ ምንም ሳይሆን ይሠራል? ሰርቪስ ላደርገው ወይም ቢበላሽ ላሠራው እችላለሁ? የሚለው ነው።
ማማርም አንዱ የጥራት መለኪያ ነው። አንዱ፣ ይህን ነገር እወደዋለሁ ይላል። ለምን ወይም በምን ወደድከው? ሲባል ምክንያት የለውም። “በቃ እወደዋለሁ” ነው መልሱ። ሌላው ደግሞ ብዙዎቹን የጥራት መመዘኛዎች ቢያሟላም “ይህን ነገር አልወደውም” ሊል ይችላል። የሚጠላበትን ምክንያት ግን አያውቀውም። እንግዲህ በእነዚህ መመዘኛዎች ለክተን ነው አንድን ነገር ከፍተኛ ጥራት ያለው ወይም ጥራቱ ዝቅተኛ ነው ማለት የምንችለው። ጥራት ምንድነው? ስትለኝ ጥያቄው ቀላል መልሱ ግን ሰፊ ነው ያልኩህ ለዚህ ነው። እኛ ስለጥራት (ኳሊቲ) ሁለት ኮርስ ነው የምንሰጠው። በ15 እና 20 ደቂቃ ስለጥራት አውርተን አንጨርስም። ታዋቂው የዓለማችን ሳይንቲስት አልበርት አነስታይን፤ “አንድን ነገር በቀላሉ ለመንገደኛ ሰው ማስረዳት ካልቻልክ ሥራህን አታውቀውም ማለት ነው” እንዳለው እንዳይሆንብኝ እፈራለሁ።
ህብረተሰቡ ስለጥራት ያለው ግንዛቤ ምን ይመስላል?
ኅብረተሰብ የሚለዋወጥ (ዳይናሚክ) ስለሆነ ብዙ ጊዜ ይቀያየራል። ከባላገር ልነሳ፤ የጥራት ፅንሰ ሐሳብ (ኮንሰፕት) አላቸው ወይ? አዎ! በሚገባ አላቸው። ቤታቸው ንፁህ ነው፤ የተቀደደ ልብስ በመርፌ ጥርቅም አድርገው ሰፍተው ነው የሚለብሱት፤ ቤታቸውን አዛባ ለቅልቀው ነው የሚኖሩት። መደብ አለች፣ ጓሳ ትነሰነሳለች፤ በሳምንቱ ተጠርጐ ይስተካከላል፤ አቅማቸው የፈቀደውን ሁሉ ያደርጋሉ። ጥራት (ኳሊቲ) ፎቅ ቤት ውስጥ መኖር ማለት አይደለም። ከብቶቻቸውን ጧት በጊዜ ያስወጣሉ፤ ማታ በጊዜ ያስገባሉ። እሳታቸውን በጊዜ ያዳፍናሉ፤ ጧት ደግሞ በጊዜ ተነስተው ያነዳሉ። እነዚህን ባለሙያ እንላቸዋለን። በባላገር ሚስት ስትመርጥ፣ በጧት ጭስ ከሚጨስበት ቤት ምረጥ ነው የምትባለው። እናቲቱ ባለሙያ ከሆነች ልጅቱም ባለሙያ ትሆናለች ነው ሃሳቡ። ባላገር ውስጥ የጥራት ፅንሰ ሐሳብና አመለካከት (ኮንሰፕት) አለ። ይህ አመለካከት ግን ማደግ አለበት።
ከተማ ውስጥስ እንዴት ነው? ከተማ ውስጥ የጥራት ፅንሰ ሐሳብ በጣም ትንሽ ነው። ሁሉም ሰው የጥራት ፅንሰ ሐሳቡን መንግሥት ላይ ጥሎታል። ደጁ ላይ ቆሻሻ እያየ መንግሥት ይጥረገው ብሎ ያልፋል። አጠገቡ ያለ ቦይ ተደፍኖ እያየ “የመንግሥት ሠራተኞች ይጥረጉት” ብሎ ይሄዳል። ከቤቱ ጠርጐ ያወጣውን ቆሻሻ ፊት ለፊቱ ባለ ቦይ ውስጥ ይጥላል፤ ውሃ የጠጣበትን መያዣ የትም ይወረውራል። ኧረ ብዙ ጉድለት ይታያል። መሠራት ያለበት ነገር አልተሠራም።
ጥራት የሚቆምባቸው ሁለት ምሰሶዎች አሉ። አንደኛው መሠረታዊ ሐሳብ “Keep and try the first time and every time”  ይላል። አንድን ሥራ ከመጀመሪያ አንስቶ በትክክል መሥራት የሚል ነው መሠረተ ሐሳቡ። ለስህተት ምንም ዕድል ያለመስጠት። “ቆይ በኋላ አስተካክላለሁ” ማለት በፍፁም አይገባም። ሁለተኛው የጥራት መሠረተ ሐሳብ፣ “There is always a way for improvement” የሚል ነው። ለመሻሻል ሁልጊዜ ዕድል አለ ማለት ነው። ዛሬ ከምሠራው ሥራ፣ ነገ የምሠራው የተሻለ መሆን አለበት። እነዚህ መሠረታዊ ሐሳቦች ሲጣመሩ፣ አንደኛ ጠንቃቆች እንሆናለን፤ ጊዜም ሳናባክን እንሠራለን።
ለምሳሌ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በታሪኩ የቴክኒክ ችግር ገጥሞት አያውቅም፤ የምንኮራበት አየር መንገድ ነው። ነገር ግን ብዙ ጊዜ በመዘግየት ይታማል። መዘግየት አለ ማለት ነው። ለምንድነው የሚዘገየው? ብለን ስንጠይቅ They do it the second time ማለት ነው። በመጀመሪያው ጊዜ በትክክል ሠርተውት ቢሆን ኖሮ መዘግየት አይፈጠርም ነበር። መጀመሪያ ቴክኒሻኑ ይሠራል፣ ከዚያም ተቆጣጣሪው ይመጣና “ይኼ ትክክል አይደለም” ይላል። ቴክኒሻኑ “ኦ ለካስ ይህቺ አልተስተካከለችም” ይልና ያስተካክላል። ስለዚህ በመጀመሪያውና በሁለተኛው ማስተካከል መኻል ያለው ጊዜ መዘግየትን ይፈጥራል። መዘግየት ደግሞ ጥራትን ያስተጓጉላል።
ሁለተኛው ምሰሶ ለመሻሻል ዕድል መስጠት ነው። ይህም ሁልጊዜ ከሌላው መማር እንደሚችልና እንደሚሻሻል የሚያሳይ ነው። ከአንተ ጋር ስንነጋገርና “ይህ ሰው በዚህ ጉዳይ ላይ የተሻለ ሐሳብ ሊኖረው ይችላል” ብዬ ማሰብ ስጀምር፣ አከብርሃለሁ። ደንበኛዬ ነህና ካንተ እውቀት እወስዳለሁ። ዛሬ ከአንተ ጋር ስለዋልኩ እውቀት አግኝቼ እሄዳለሁ ማለት ነው። እነዚህ ሁለቱ የጥራት ዋነኛ መሠረተ ሐሳቦች፣ ምሰሶዎች (ፒላርስ) ናቸው።
እነዚህ የጥራት ምሰሶዎች በአገራችን አሉ? ከተባለ፣ የሉም ማለት ይከብዳል። አሉ፣ ግን በጣም በጥቂቱ ነው ያሉት። በሥራዬ አጋጣሚ ብዙ አገሮች ዞሬአለሁ። በአሜሪካና በአውሮፓ የትም አገር ሽንት ቤት ውስጥ “ከተጠቀማችሁ በኋላ ውሃ ልቀቁ” የሚል ጽሑፍ አይቼ አላውቅም። ወደ አገራችን ስንመጣ ግን “ትልቅ” የተባለ ሆቴል ውስጥ ይሄ ማሳሰቢያ ተጽፎ ይታያል። ምን ማለት ነው? እኔ ሽንት ቤቱን ከተጠቀምኩ በኋላ ቀጥሎ የሚመጣ ሰው ደንበኛዬ ነው። እኔ ሽንት ቤቱን በምጠብቅበት ሁኔታ እሱም እንደሚጠብቅ አውቄ እሱን ማክበር አለብኝ። በምዕራብ አገሮች ይህ ስለገባቸው በት/ቤት መፀዳጃ ቤቶች ውስጥ እንኳ አይጻፍም። እኛ አገር ለምን ይጻፋል? ለጥራት ያለን ግንዛቤ ዝቅተኛ ስለሆነ  ነው። ይህን ይህን ሳይ “ምን ይሻላል?” የሚለው ብዙ ጊዜ ያሳስበኛል። አዲሱ ትውልድ ስለጥራት ያለው ግንዛቤ እንዲያድግ ካስፈለገ ያለን አስተሳሰብ ሙሉ በሙሉ መለወጥ አለበት።
ለምሳሌ እኔና አንተ ደንበኞች ነን። እኔ አንተን ለማስደሰት፣ እኔ እሱን ብሆን ኖሮ እንዴት እንዲሆንልኝ እፈልጋለሁ? ሰዓት እንዲያከበርልኝ እፈልጋለሁ። ጥያቄዬ ሁሉ በቅንነት እንዲመለስልኝ እፈልጋለሁ… በማለት ማሰብ አለብኝ። ይህን ካደረግሁ አንተ ደስ ይልሃል። በሁሉም ቦታ ደንበኞቻችንን ማስደሰት ስንፈልግ፣ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ “እናንተ እንዲደረግላችሁ የምትፈልጉትን እናንተም አድርጉላቸው” የሚለውን ማሰብ ያስፈልጋል። ይሄ አባባል የጥራት ዋነኛ መመሪያ ነው። ይሄንን መመሪያ መተግበር ወሳኝ ነው። እንግዲህ የጥራት ፅንሰ-ሃሳብ እንዲተገበር ከታች ከጽዳት ሠራተኛው እስከ ላይኛው ባለሥልጣን ድረስ የልቡና ውቅር (ስትራክቸር)፣ የአስተሳሰብና የአመለካከት ለውጥ (የፓራዳይም ሺፍት) መደረግ አለበት።
ለጥራት ያለ የአመለካከት ለውጥ (ፓራዳይም ሺፍት) እንዴት ነው የሚመጣው?
እንደ ዕንቁላልና ዶሮዋ የተሳሰረ ነው፤ ጥራትና ምርታማነት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ናቸው። ጥራት ከሌለ ተወዳዳሪነትና ዕድገት የለም። በመጀመሪያ በኅብረተሰቡ ውስጥ ግንዛቤ መፍጠር ያስፈልጋል። ሰው ሁሉ እንዲያውቀው ማድረግ የግድ ነው። ጋዜጦች፣ ቴሌቪዥኖች፣ ሬዲዮኖች፣ በአጠቃላይ ሚዲያው፣ የጥራት ሐሳብ በኅብረተሰቡ ውስጥ በሚገባ እንዲሰርጽ በብዛት መሥራት አለባቸው። እኔ እግር ኳስ በጣም ስለምወድ በየሬዲዮ ጣቢያው ስለኳስ ሲያወሩ በጣም ደስ ይለኛል። ነገር ግን ለስፖርቱ የተሰጠው ጊዜ ግማሽ ያህል እንኳ የጥራትን መሠረተ ሐሳብ ለማስረፅ ቢውል አገሪቷ የት በደረሰች።
መጀመሪያ ግንዛቤ መፍጠር ነው፤ ቀጥሎ እርምጃ መውሰድ። ሰው ግንዛቤ ካገኘ በኋላ እያንዳንዱ ግለሰብ መለወጥ አለበት። በሶስተኛ ደረጃ ራሱን እያሻሸለ ሳለ መታገል አለበት። ለምሳሌ ታክሲ ውስጥ ተደራርባችሁ ተቀመጡ ሲባል ትክክል ስላልሆነ መቃወም አለበት። “ፋዘር ወይም ማዘር ጠጋ በሉ” ማለት ከጥራት መሠረተ ሐሳብ ጋር አይሄድም። ስለዚህ መቃወም አለበት። በየትም ቦታ ቢሆን እያንዳንዱ ግለሰብ ትክክል ያልሆነ ነገር ሲያይ ዝም ማለት የለበትም። ህብረተሰቡ መምራት አለበት። ይህንን ለማድረግ ደግሞ ግንዛቤው መዳበር አለበት። ትያትረኞች ጸሐፊዎች፣ ገጣሚዎች፣ አርቲስቶች፣ …. ጥራት ላይ መሥራት አለባቸው። ትያትር በህብረተሰቡ ውስጥ የበለጠ ተፅዕኖ መፍጠር የሚችለው በጥራት ላይ ሲሰራ ነው። ስለ ጥራት ማስተማርያ የአየር ሰዓት መኖር አለበት። ስለ ጥራት ካስተማርን በኋላ እርምጃ መውሰድና ሮል ሞዴሎች (አርአያዎች) መፍጠር አለብን።
ለምሳሌ አበበ ቢቂላን ብንወስድ በሩጫ ጥሩ ሮል ሞዴል ነው። ግን ለቢዝነሱ ጥሩ ሞዴል አይደለም። ከአበበ በኋላ ኃይሌ ገ/ሥላሴ መጣ። ኃይሌ ጥሩ የቢዝነስ ሞዴል ስለሆነ ከእሱ በኋላ የመጡት በሆቴልና በሌላ የቢዝነስ ዘርፍ ተሰማሩ። በጥራትም ሮል ሞዴሎች ስለሚያስፈልጉን መሸለምና ማበረታታት ያስፈልገናል። ለዚህ ደግም የሽልማት ድርጅት ያስፈልገናል። ይህ ነገር በህብረተሰቡ ውስጥ ሲደጋገም ባህል ይሆናል። ይህቺ አገር ምን ያሳድጋታል ብትለኝ፣ ጥራትና ምርታማነትን ማሳደግ…  ነው የምለው።
በዚህ ረገድ አዲሱ ትውልድ (ወጣት፣ ሕፃናት፣ ሴቶች) ላይ መሠራት አለበት።  ለሴቶች ቦታና ዋጋ መስጠት ይገባል። በት/ቤቶች ደግሞ አሁን ያሉት መምህራን ከጥራት ግንዛቤ ውጭ ስለሆኑ፣ የአሰልጣኞች ስልጠና ፕሮግራም ያስፈልጋል። የትምህርት ካሪኩለሙም መቀየር (የፓራዳይም ሺፍት ማድረግ) ይኖርበታል። የሽምደዳ ካሪኩለም መቀየር አለበት።
ልጆች፣ ተፈጥሮን ወደዋትና ተንከባክበው እንዲይዟት ማበረታታት ያስፈልጋል። እፅዋት ከተንከባከቡ በውስጡ ለሚኖሩት ነፍሳት አክብሮት ይሰጣሉ። ተፈጥሮን የሚወዱ፣ ደንበኞቻቸውን የሚያከብሩና የሚደራደሩ ወጣቶችን ማፍራት አለብን። መደራደር ስል እናቶችን ማስተማር ያለብን አንድ ነገር አለ። ልጆቻቸው እንዲያጠኑ ሲፈልጉ፤ “አጥኑ፤ ያለበለዚያ ትመታላችሁ” አይደለም ማለት ያለባቸው።
እናት፤ “አጥኑ፣ ካላጠናችሁ ቴሌቪዥን አይከፈትም”
ልጆች፤ “ስንት ቀን ነው የምናጠናው?”
እናት “በሳምንት ስድስት ቀን”
ልጆች “አራት ቀን”
እናት፤ “የለም! አምስት ቀን”… እየተባባሉ መደራደርን መልመድ አለባቸው። ከልጅነታቸው ጀምሮ መደራደር ካላስተማርናቸው አድገው የፓርቲ መሪ ሲሆኑ አይደራደሩም። “ወይ እሞታለሁ፤ ወይ እገለብጣለሁ” ነው የሚሉት። የጥራት ጉዳይ ይህን ያህል ጥልቅ እንደሆነ አንባብያን እንዲረዱልኝ እፈልጋለሁ።
በአገራችን የሚታየውን የምርትም ሆነ የአገልግሎት ጥራት ማነስ እንዴት ይገልጹታል?
 በእኛ አገር አብዛኛውን ጊዜ ሰራተኛው ችሎታ የለውም ሲባል እንሰማለን። ነገር ግን ከ80 እስከ 90 በመቶ የጥራትና የምርታማነት ችግር ሲስተሙ (አሰራሩ ላይ) ነው። ስለዚህ ሲስተሙ መለወጥ አለበት። ሲስተሙ ትክክል ሲሆን ሠራተኛው ትክክል ይሆናል። ለምሳሌ፣ ውልና ማስረጃን ያየን እንደሆነ ሰራተኞቹ አልተቀየሩም። ወይም ፈረንጅ አልመጣም። ሲስተሙ ስለተስተካከለላቸው፣ ሁለት ቀን የሚፈጀውን ሥራ በ30 ደቂቃ ይሠሩታል። ነገር ግን ሲስተሙ ተስተካክሎ ብቻ መቆም የለበትም። ልምድና ባህል መሆን አለበት። አንድ ሰው ቆሞ እንዲህ አድርግ፣ አታድርግ ማለት የለበትም። ያለበለዚያ ወደ ኋላ ይመለሳል።
ፋብሪካዎችም የሲስተም ችግር አለባቸው። እሱንም ማስተካከል ያስፈልጋል። ከዚህ ጋር ሌላው አስፈላጊ ነገር ስልጠና ነው። በተለይ ስለ ጥራትና ምርታማነት ስናወራ ከስልጠና ውጭ ሊሆን አይችልም። የስልጠና ክፍለ ጊዜ ያላቸው ድርጅቶች ስንት ናቸው? ስንል በጣም ጥቂት ናቸው። አቶ ታዲዮስ ሐረገወርቅ ምክትል ሚኒስትር ከነበሩበት ጊዜ ጀምሮ ዩኒቨርሲቲዬን እየወከልኩ በስልጠና ጉዳይ ስለምሰራ ብዙ ድርጅቶችን አይቻለሁ። አብዛኞቹ የስልጠና ክፍለጊዜ የላቸውም። ምናልባት አንድ ሰው “የሥልጠና ኃላፊ” ተብሎ ሊቀመጥ ይችላል። ነገር ግን ጥራት ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ቴክኖሎጂዎች ሲወጡ፣ የሥልጠና ክፍል ኖሯቸው መመሪያ አዘጋጅተው፣ ቤተመጻሕፍት አስቀምጠው ሰራተኞቻቸውን የሚያሰለጥኑ ድርጅቶች ጥቂት ናቸው። ቴሌ፣ አየር መንገድ፣ አውራ ጎዳና፣ ከክልሎችም እንዲሁ… ይኼ ምንድነው የሚያሳየው? የጥራት ፍልስፍና ፅንሰ ሐሳብ አልገባንም ማለት ነው። ሥልጠናን ሲስተማችን ውስጥ አላስገባንም።
ማነው ሲስተሙን መቀየር ያለበት?
የሚገርመው ነገር የግሉ ዘርፍ ነበር ቢፒአር የተባለውን የለውጥ ሂደት መምራት የነበረበት። ቢፒአር አተገባበሩ ትክክል ከሆነ መሰረታዊ አሰራሩ ጥሩ ነው፤ አምንበታለሁ። ይህ የለውጥ ሐሳብ ከግሉ ዘርፍ መምጣት ነበረበት። ነገር ግን መንግሥት ቀደመው። ለምን? ቢባል፣ በታዳጊ አገር ያለው የግሉ ዘርፍ ዕድሜ ጨቅላ ስለሆነና ስላልጎለበተ ነው። ስለዚህ ኃላፊነቱን መንግሥት ወሰደ። መንግሥት ይህን ኃላፊነት ሲወስድ ግን ሁሉንም እኔ መስራት አለብኝ ማለት የለበትም። ይህን የሚሰሩ የግል ዘርፎችን አደራጅቶ እየሰሩ ከስህተታቸው እንዲማሩ መልቀቅ ያለበት ይመስለኛል። እርግጠኛ ያልሆንኩት በምርምርና በዳታ የተደገፈ መረጃ ስለሌለኝ ነው።
የጥራት ፍልስፍናን መሠረተ ሐሳብ ተግባራዊ በማድረግ የተለወጠና ለአብነት የምንጠቅሰው አገር አለ?
አዎ! ለምሳሌ ሲንጋፖርን መጥቀስ እንችላለን። ሲንጋፖር እ.ኤ.አ በ1966 ነው ከቅኝ ግዛት ነፃ የወጣችው። 50 ዓመት እንኳ አልሞላትም። ከዚያን ጊዜ አንስቶ እስከ 1980 ድረስ ሲስተም እያስተካከሉ ቆዩ። ከዚያም ሊ ኳን የተባለ ጠቅላይ ሚኒስትራቸው “ምርታማነት የአዕምሮ መቀየር ነው። ከአሁን ጀምሮ በዚህ አቅጣጫ ነው የምንሄደው” በማለት አወጀ። ይህን የለውጥ ሂደት የሚመራ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የሚመራ ኮሚቴ አቋቋመ።
ለአምስት ዓመት የህብረተሰቡን የምርታማነትና የጥራት ግንዛቤ ሲያሳድጉ ቆዩ። ቴሌቪዥኑ፣ ሬዲዮው፣ ጋዜጣው፣ መጽሔቱ፣ ዘፈኑ… በየመንገዱ ላይ የሚሰቀሉትና በየግድግዳው የሚለጠፉት ፖስተሮች፣ .. ሁሉ የቆየ አመለካከት መለወጥና አዲሱን የለውጥና የዕድገት ትሩፋቶች ማስተማር ነበር ሥራቸው። ከዚህ በኋላ ወደ ተግባር እርምጃ ገቡና የለውጥ ሂደቱን የሚመሩ የተለያዩ ተቋማትን አቋቋሙ። በዚህ ዓይነት ሲሰሩ ቆይተው የሕዝባቸውን አዕምሮ ቀየሩት። ከ20 ዓመት በኋላ እ.ኤ.አ በ2000 ዓ.ም 12 መመዘኛዎች ባሉት ግሎባል ፕሮዳክቲቪቲ ኢንዴክስ በተባለው የምርታማነት መለኪያ ከዓለም አገራት ጋር ተወዳድረው 3ኛ ወጡ። ከዚያ በኋላ ደግሞ ለውጥ ያገኙበትን አሰራር (ሲስተም) የራሳቸው አደረጉት።  የህልውናቸው አካልና መገለጫ ሆነ። በመቀጠል ደግሞ የራሳቸው ባደረጉት ሲስተም አዲስ ነገር ወደ መፍጠር (ኢኖቬሽን) ገቡ።
በሲንጋፖር አንድ ቢሮ አንኳኩተህ የምትፈልገውን ስትጠይቅ፣ የተቀበለህ ሰው ጉዳዩ የማይመለከተው ከሆነ፣ የሚመለከተው ጋ ይወስድሃል ወይም ወደሚመለከተው ሰው ጋ ወደሚወስድህ ሰው ያደርስሃል እንጂ “አይ! እኔ አላውቅም” አይልህም። የአገር ጉዳይ ነዋ! የታክሲ ሹፌሩ ከአየር ማረፊያ ወደምታርፍበት ሆቴል ሲወስድህ፣ ስለአገሩ እያወራልህ ነው። “ይህ ቦታ በፊት እንዲህ ነበር፤ እኛ ነን እንዲህ ያሳመርነውና የለወጥነው። ይህ ደግሞ …” እያለ በማውራት ሆቴል ያደርስሃል። እሱ ምን ሰራ? ብትል በሙያው በአቅሙ “ይህ የመንግሥት ሳይሆን የእኔ ጉዳይ ነው” በማለት በዜግነቱ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት ተወጥቶ ይሆናል። ይኼ ነው የምርታማነት ፅንሰ ሀሳብ።  የሚገርመው ነገር እንደ እኛው ኋላቀር የነበረችው ሲንጋፖር እዚህ “ተአምራዊ” የሚመስል ፈጣን ዕድገት ላይ የደረሰችው በ48 ዓመት ነው።    
ድሮ የጃፓን ምርት ጥራት እንደሌለው ለመግለጽ፣ “ኪሽ ኪሽ የጃፓን ዕቃ ወድቆ የማይነሳ” ወይም “አወይ ሞሶሎኒ አወይ ሞሶሎኒ ተሰባብረህ ቀረህ እንደ ጃፓን ሶኒ” ይባል ነበር። አሁን ግን ጃፓን የዓለምን ኢኮኖሚ ከሚመሩት ቀዳሚ አገራት አንዷ ነች። እንዴት ለዚህ በቃች?
ጃፓንም እንደ ሲንጋፖር ምሳሌ የምትሆን አገር ናት። እንደተባለው ምርቷ ጥራት የሌለው ነበር። ከ2ኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ---------- የተባሉ አሜሪካውያን በአገራቸው ስለጥራትና ስለምርታማነት ጮኸው ጮኸው የሚሰማቸው ቢያጡ፣ ወደ ጃፓን ሄዱ። እዚያም 150 ሥራ አስኪያጆችን ሰብስበው ስለጥራትና ምርታማነት አወሯቸው። “አሁን የነገርናችሁን ተግባራዊ ካደረጋችሁ በአምስት ዓመት ውስጥ ለውጥ ታመጣላችሁ” አሏቸው። እነዚያ ሥራ አስኪያጆች ጠንክረው በመስራታቸው በአምስት ዓመት ሳይሆን በሦስት ዓመት ለውጥ አመጡ። እነጃፓንንና ሲንጋፖርን ከቀየረ፣ የእኛንም አገር ይቀይራል ማለት ነው።
ወደዚያ የሚወስደው ጉዞ ተጀምሯል?
ጥሩ ተስፋ ሰጪ ጅምሮች አሉ። ካይዘን በጣም ጥሩ ጅምር ነው። እንዲህ ዓይነት ጅምሮችን ማነቃቃትና ማበረታታት፣ ከፍ እንዲሉና እንዲልቁ ማገዝ፤ ሰራተኞቹ ደግሞ በፍፁም የተለወጡ እንዲሆኑ በየጊዜው ሥልጠና፣ እውቅና፣ አክብሮትና ሽልማት መስጠት ያስፈልጋል።

Saturday, 19 April 2014 12:04

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

እንኳን ለብርሀነ ትንሳኤው አደረሳችሁማ! ያጣናቸው፣ የወደቁብን መልካም ነገሮች ሁሉ ትንሳኤ ያድርግልንማ!
ታላቁ መጽሐፍ ላይ… “ከእኔ ጋር እጁን በወጭቱ ያጠለቀ፣ እኔን አሳልፎ የሚሰጥ እርሱ ነው፣” ተብሏል። በዚህ ዘመንም፣ በዚች ምድርም እጁን አብሮ በወጭት አጥልቆ አሳልፎ የሚሰጥ መአት ነው። ልክ የሆነ ድንገተኛ ግዝት የወረደብን ይመስል…እሱ ነው/እሷ ነች አይነት የአመልካች ጣት ጥቆማ ዘመን ሆኗል። ባይማማሉም ተማምነው አብረው ያፈሩትን ገንዘብ፣ አብረው ያቀዱትን መልካም ለብቻ ማድረግም በተዘዋዋሪ አሳልፎ መስጠት ነው። ከመላእክት እኩል ጻድቅ በመምስል፣ በታላቅ ትህትና ‘አንገትን በመስበር’ ተለሳልሶ ገብቶ የሰውን ህይወት አቆርፍዶ ፈትለክ የሚል መአት ነው። እናላችሁ…አሳልፎ መስጠት በብዙ መልኩ ይከሰታል።
እናላችሁ…“…እኔን አሳልፎ የሚሰጥ እርሱ ነው፣”  እንደተባለው ሁሉ እውነትም
“…የምስመው እሱ ነው ያዙት፣ ተጠንቅቃችሁም ውሰዱት…” ተብሎም ተጽፏል።
ታዲያላችሁ…ዘንድሮም “የምስመው እሱ ነው…” እያለ የምናስወስድ መአት ነን።
የመተማመን ነገር ጠፍቶ፣ ጥላችንን እየተጠራጠርን…‘ከወዳጆቼ ጠብቀኝ ጠላቶቼን እኔ እጠብቃቸዋለሁ’ የምንለው ‘ስሞ የሚያስወስድ’ በመብዛቱ ነው።
ምሎ ተገዝቶ ‘ነፋስ የማይገባበት ወዳጅነት’ ከተባለ በኋላ… አለ አይደል… ትንሽ ቆይቶ በ“የምስመው እሱ ነው…” አይነት ወደ ቅልጥ ያለ ባላጋራነት ይለወጣል።
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ብዙ ጊዜ እንደምንለው…እዚህ አገር ‘ሪሰርች’ ምናምን የሚባል ነገር የተለመደ ነው ማለቱ ያስቸግራል። እናላችሁ…ዘንድሮ መኖራቸውን እንኳን ነገሬ ሳንላቸውና የግለሰቦች ጉዳዮች ናቸው በሚል ችላ ብለናቸው የነበሩ እኩይ ባህሪያት በአጭር ጊዜ ለምን በዚህ ፍጥነት የተስፋፉበትን ምክንያት አጥንተው የሚነግሩን ሰዎች መጥፋታቸው ያሳዝናል። እናማ…“የምስመው እሱ ነው…” አይነት መከዳዳት ከዋናዎቹ ባህሪያቶቻችን አንዱ የሆነበትን ምክንያት የሚያስረዱን እንፈልጋለን።
እኔ የምለው….እንግዲህ ጨዋታም አይደል… የ‘ሪሰርች’ ነገር ካነሳን አይቀር ምን መሰላችሁ…በብልቃጦችና በኬሚካሎች የተሞሉ ቤተ ሙከራዎች ውስጥ ባይሆንም እዚህ አገር በእርግጥ ቅልጥ ያለ ‘ሪሰርቾች’ ይደረጋሉ! ልክ ነዋ…“ስማ ባሏ ፊልድ የሚወጣው መቼ፣ መቼ እንደሁ እስቲ ሠፈር አካባቢ አጠያይቅና አጣራልኝ…” “የጫማዋ ቁጥር ስንት እንደሁ ከጓደኞቿ ሰልልኝ…” ሁሉ ‘ሪሰርች’ ነው።
እናላችሁ…በታላቁ መጽሐፍ እንዲህም ተብሏል…
“በዚች ሌሊት ሁላችሁ በእኔ ትሰናከላላችሁ፣ እረኛውን እመታለሁ፣ በጎችም ይበተናሉ የሚል ተጽፎአልና...”
“ዼጥሮስም ሁሉም ቢሰናከሉ እኔ ግን ከቶ አልሰናከልም አለው። እየሱስም፣ እውነት እልሀለሁ ዛሬ በዚች ሌሊት ዶሮ ሁለት ጊዜ ሳይጮህ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ አለው።”
እናማ…በአሁኑ ጊዜም… አለ አይደል… “አህያ ወደቤት ውሻ ወደ ግጦሽ በሆነበት ዘመን “ሁሉም ቢሰናከሉ እኔ ግን ከቶ አልሰናከልም” አይነት ነገር እያልን በአፍ ‘ቲራቲር’ የምንደልል መአት ነን። የሚደለለውም መአት ነው።
እናማ…ያሰቡትን እስኪፈጽሙ፣ ‘የልባቸው እስኪደርስ’ ሲምሉ፣ ከርመው የቁርጥ ቀኑ ሲመጣ እንዲህም ይሆናል…
“ከሊቀ ካሀናቱ ገረዶች አንዲቱ መጣች፣ ዼጥሮስም እሳት ሲሞቅ አይታ ተመለከተችውና፡— አንተ ደግሞ ከናዝሬቱ እየሱስ ጋር ነበርህ አለችው። እርሱ ግን የምትዪውን አላውቅም፣ አላስተውልምም ብሎ ካደ።”
“አላውቅም አላስተውልምም…” ብሎ ሽምጥጥ አድርጎ መካድ ዘንድሮ የክህደት ሳይሆን ጭርሱን የብልህነት መለኪያ ሆኗል። በዚህም የለፋበትን፣ ላቡን ያፈሰሰበትን የሚያጣ ስንቱ እንደሆነ ቤቱ ይቁጠረው።
 በታላቁ መጽሐፍ እንዲህም ተብሏል…
“ይሁዳ ሆይ በመሳም የሰውን ልጅ አሳልፈህ ትሰጣለህን?” አዎ፣ አሁንም የምንለው በመሳም አሳልፋችሁ ትሰጡናላችሁን?
በመሳም እሴቶቻችንን፣ ክብራችንን አሳልፋችሁ ትሰጡብናላችሁን?
በመሳም የ‘ፈረንጅ’ መዘባበቻ ታደርጉናላችሁን?
…እንላለን።
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…እዚሀ አገር ይሄ ‘ፈረንጅ’ እየተከተሉ ባልታየ ትርኢት ማጨብጨብ፣ ባላስነጠሰው መሀረብ ማቀበል፣ ባላንገዳገደው “እኔን ይድፋኝ!” ማለት፣ ባልዘነበ ዝናብ፣ ባልከረረች ፀሀይ ዣንጥላ መዘርጋት ምናምን ነገር ላይለቀን ነው! (አንዳንዶቻችን እኮ…አለ አይደል… ማጨብጨብ ብቻ ሳይሆን በሊዝ ለ‘ፈረንጅ የተላለፍን’ ይመስለናል!)
የምር እኮ…ግርም የሚል ነገር ነው። ጤፍ አሪፍ ምግብ ለመሆኑ የፈረንጅ ‘ደረቅ ማህተም’ እና ቡራኬ ለምን እንደሚያስፈልገን አይገባኝም።
“ፈረንጅ አደጋችሁ ብሎናል…”
“ፈረንጅ ህዝባችሁ ጨዋ ነው ብሎናል…”
“ፈረንጅ ግሩም ባህል አላችሁ ብሎናል…”
“ፈረንጅ በአክሱም ሀውልት ተደንቄያለሁ ብሎናል…”
“ፈረንጅ ሴቶቻችሁ ቆንጆዎች ናቸው ብሎናል…”
ፈረንጅ!… ፈረንጅ!… ፈረንጅ!…
እናማ…የምድሩንም የሰማዩንም ለፈረንጅ ሰጥተን…እልፍኛችንንና ጓዳችንን ባዶ እያደረግናቸው ነው።
የባህል ልብሶቻችን እርፍና ለመመስከር ለምን በፈረንጅ አንደበት እስኪነገር፣ ለምን በፈረንጅ ወይዘሮ እስኪለበስ እንደምንጠብቅ ግራ ግብት አይላችሁም! ፈረንጅ የሀበሻን ልብስ ወደደው፣ አልወደደው የልብሱን እርፍና አይጨምረው፣ አይቀንሰውም። (ስሙኝማ…ያኔ “አይሞቀንም አይበርደንም…” ይባል የነበረው ነገር…ናፈቀንሳ! ነገርየው እንዴት ሆኖ ይሆን… ነው ወይስ ሁሉም ነገር በሰሜን ዋልታ በረዶ ተውጦ አረፈው!)
እናላችሁ…ለታሪካዊም ሆነ ባህላዊ እሴቶቻችን ደረጃ ለማውጣት የፈረንጅን በጎ አመለካከት ለምን እንደምንጠብቅ ግራ የሚገባ ነው። አሁን፣ አሁን “ለምን መሬት ነክቷችሁ…” እያልናቸው ያሉ የሙዚቃ ሰዎቻችን እኮ ፈረንጅ አገር ሽልማቶች ከማግኘታቸው በፊት እዚህ ለአሥርት ዓመታት አብረውን ነበሩ እኮ! እናማ… ምነው ያኔ ዓይናችን አላያቸው አለ!…ምነው ያኔ የሙዚቃ ሰዎቻችንን ክህሎቶች በእኛው አንደበት ለዓለም መለፈፍ አቃተን!
አሁን ደግሞ “ጤፍ ዓለም አቀፍ ምግብ ልትሆን ነው…” ምናምን እየተባለ እየተቀባበልነው ነው። እንደውም “የጤፍን ዓለም አቀፍ ዝና ማግኘት ምክንያት በማድረግ ጤፍ የኩራታችን ምንጭ…” ምናምን የሚባል ፌስቲቫል እንዳይዘጋጅ ፍሩልኝማ።
እኔ የምለው…በዛ ሰሞን የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ፈረንጅ ይሁን የአገር ሰው ምናምን ሲባል ከረመና…ፈረንጅ ሆነና አረፈው ተብለን ነበር! ፈረንጁ ከመጡ በኋላ ደግሞ ሳይስማሙ ቀረ ተባለ። “ይሁና!” ከማለት ውጪ ምን ማለት ይቻላል! (“ይሁና! ይሁና!” ምናምን የሚለው ዘፈን ግጥሙ ለጊዜው እንዲመች ሆኖ ተስተካክሎ ይዘፈንልንማ!)
እናላችሁ…የፈረንጅ አሰልጣኝ ምናምን ሲባል ምን እንላለን መሰላችሁ…እውን ለኢትዮጵያ ቡድን ደረጃ የሚመጥን ሀበሻ አሰልጣኝ ጠፍቶ ነው! ደግመን ደጋግመን የምንጠይቀው ጥያቄ ነው። (ሀሳብ አለን… ‘ፈረንጅ’ አሰልጣኝ ከተቀጠረ በኋላ … ድንገት ፊፋ የባሰ ቁልቁል ካወረደን… “እኛ እኮ ችሎታው ጥሩ መስሎን ነበር…”   “ቡድናችንን ለሞሮኮ ያደርስልናል ብለን ነበር…” ምናምን አይነት ‘ቀሚስ አደናቀፈኝ’ አይነት ነገሮች ከመስማት ይሰውረንማ! ስሙኝማ…መጥተው የሄዱ የፈረንጅ አሰልጣኞች ሠላሳ ስምንት ምናምን ይሆናሉ ነው የተባለው! ‘የቀድሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ፈረንጅ አሰልጣኞች’ የሚል ማህበር ለማቋቋም አይበቁም!)
ታዲያላችሁ…
ሰዉ ሁሉ ሲስማማ ሲፋቀር ሲዋደድ
ማታለል ሳይበዛ መዋሸት በገሀድ
በአፍ ቢላዋነት ሳይሆን ሰውን ማረድ
ያ ደጉ ቀን ጠፋ እኛ ሳንወድ በግድ።
ተብሎ ተዚሞ ነበር። የጠፋው ደግ ቀን ትንሳኤን ያፍጥልንማ!
በድጋሚ እንኳን ለብርሀነ ትንሳኤው አደረሳችሁ! የሰላምና የጤንነት የበዓላት ሰሞን ያድርግላችሁ!
“የምስመው እሱ ነው…” ከሚሉ ‘ስሞ አሳላፊ ሰጪዎች’ ይሰውራችሁማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

እንኳን አደረሰህ …
እንኳን አብሮ አደረሰን። .ለአዲስ አድማስ የዝግጅት ክፍልና ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች መልካም በዓል እመኛለሁ።
ፆም እንዴት ነበር?
በጣም አሪፍ ነበር። አሁን ደግሞ..የህማማት ሳምንት ነው።  ጥሩ ጊዜ እያሳለፍኩ ነው።
‹‹ጎሳዬ ዘፈን አቆመ›› የሚል ነገር ሲናፈስ ቆይቷል። እውነት ነው እንዴ?
ለስራዬ አስፈላጊ ካልሆነ በስተቀር ማህበራዊ ድረ ገፆችን አልጠቀምም። በፈረንጆች ኤፕሪል መጀመሪያ አካባቢ ነበር ይሄ ወሬ በፌስ ቡክ መናፈሱን ወዳጆቼ የነገሩኝ። በኋላ ላይ እኔም ራሴ ፌስ ቡክ ላይ አየሁት። እነዚሁ ‹‹ዘፈን አቆመ፣ ሀይማኖቱን ቀየረ›› ብለው ያስወሩ ሰዎች መልሰው ‹‹ኤፕሪል ዘ ፉል ነው›› አሉ። ችግሩ ግን “ኤፕሪል ዘ ፉልን” የማያውቅ ሰው ይኖራል። ነገሩ አድናቂዎቼን የሚያሳዝን ስለነበረ፣ በወቅቱ በጣም ተበሳጭቼ ነበር።
ወሬው ሲናፈስ የት ነበርክ? አውስትራሊያ እንደነበርክ ሲነገር ነበር…
ይኼም የተሳሳተ መረጃ ነው። በወቅቱ እዚሁ ሀገር ውስጥ ነበርኩ። ከአንድ ዓመት በፊት አውስትራሊያ የሄድኩት። መረጃዎች ለምን እንደዚህ እየተዛቡ እንደሚቀርቡ አላውቅም። ነገር ግን እኔ ለአሉባልታና ለወሬ ቦታ አልሰጥም።
ጎሳዬ “አደራ” በተሰኘውና ከመሃሙድ ር ባወጣው  ነጠላ አልበም ላይ የገባውን ቃል አልፈፀመም፤ ከሙዚቃ ሥራ ጠፍቷል የሚሉ ወገኖች አሉ …  
ከታላላቆቹ  ከምንወዳቸውና ከምናከብራቸው ድምፃውያን ..የሙያ ቅብብሎሹን በርግጥም ተቀብለናን። እኔም አደራዬን ለመወጣት እየሰራሁ ባለበት ጊዜ ነው ጭራሽ አንገት የሚያስደፋ አንዳንድ ስም የማጥፋት ዘመቻዎች የተደረጉት። እንዲያም ሆኖ በአዲስ ስራና በአዲስ መንፈስ  ከአድናቂዎቼ ጋር ለመገናኘት ሌት ተቀን እየሰራሁ ነው። ከአንጋፋ ሙዚቀኞች ጋር ነው አዲሱን አልበሜን የሰራሁት። በአሁኑ ጊዜ ቀን ከሌት እየሰራሁ ያለሁት አዲሱን አልበሜን ነው። ምን አልባትም በቅርቡ አንድ ነጠላ ዜማ ከሙሉ አልበሜ ቀንሼ ልለቅ እችላለሁ።
የዓመት በዓል ኮንሰርቶችስ ይኖሩሃል?
የመጨረሻውን ኮንሰርት የሰራሁት የዛሬ ዓመት አውስትራሊያ ነበር። በአሁኑ ሰዓትም ከካናዳ፣ አሜሪካና የተለያዩ አረብ ሃገራት ጥሪዎች እየመጡ ነው - የበዓል ኮንሰርት እንዳቀርብ። እስካሁንም ብዙ ኮንሰርቶችን ደጋግሜ ስለሰራሁና በቆየ ስራ በተደጋጋሚ መታየት ስላልፈለግሁ ነው እንጂ ጥያቄዎች ነበሩ። የዓመት በዓል ኮንሰርት ለማዘጋጀት ሁኔታ ደግሞ በአዲሱ አልበሜ ስለተጠመድኩ አልቻልኩም። አዲሱ ስራዬ ወጥቶ በህዝቡ ውስጥ በደንብ ከተደመጠ በኋላ ግን ወደ ኮንሰርት ሥራ ልገባ እችላለሁ።
በናይት ክለቦችም መስራት ትተሃል?
የትም የለሁም፤ ምክንያቱም ቀንም ተሌት የምሰራው አዲሱን አልበሜን ነው። አድናቂዎቼ በአዲሱ አልበሜ እንዲጠብቁኝ ነው የምጋብዛቸው። 

Published in ህብረተሰብ

ኢቢኤስ፣ ሠይፉ ፋንታሁንና ግሩም ኤርሚያስ የኢትዮጵያን ህዝብ ይቅርታ ሊጠይቁ ይገባል
ሰይፉ በኢቤስን ያን ዕለት ላላያችሁ
የዛሬ ሶስት ሳምንት መሆኑ ነው…ለነገሩ በሠይፉ የኢቢኤስ ትርዒት፣ ዋናው እንግዳ አርቲስት ዓለማየሁ ታደሠ ነበር፡፡ ሠይፉ ከዓለማየሁ ጋር እዚህ ግባም የማይባል ወግ ቢጤ ከጠራረቀ በኋላ የዓለማየሁን የትወና ብቃትና አዲስ የሰራውን ፊልም በተመለከተ ምስክርነት እንዲሰጡ ኮሜዲያን ደረጄ ሃይሌና የፊልም ተዋናይ ግሩም ኤርሚያስ ተራ-በተራ ቀረቡ፡፡ ይህን ጊዜ ዋናው እንግዳ አለማየሁ ታደሰ ተረሳና ትርዒቱ የደረጄና የግሩም ሆነ፡፡ ይሁና….ይኸ ለወትሮውም ቢሆን እንጀራው የሆኑትን የጥበብ ሰዎች ባለማክበር፣ በማንጉዋጠጥና በማሸማቀቅ የሚታወቀው የሰይፉ ፋንታሁን ባህሪ ነውና ምን ያስገርማል?
ይልቁኑ ጉዱ የታየው በግሩም ኤርሚያስ ቃለ-መጠይቅ ወቅት ነው፡፡ ግሩም በዋና ተዋናይነት ተሳትፎበት በቅርቡ ለዕይታ ይበቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ በራሱ አንደበት ስለነገረን አንድ ፊልም ማውራት ጀመረ፡፡ ቆየት ብሎ የአንድን የትወና ስታይል ፈጣሪ በማጣቀስ “ከእንግዲህ የምሰራቸውን ፊልሞችና ትወናዎችን መስዬ ሳልሆን ሆኜ መጫወት እፈልጋለሁ” አለ፡፡ ከዚያም ምሳሌ አጣቅሶ እንዲህ ተናገረ፡፡ “ለምሳሌ በአዲሱ ፊልም ላይ የአደንዛዥ ዕፅ ሱሰኛ የሆነ ወጣትን ወክዬ ነው የተጫወትኩት፡፡ ታዲያ ይሄንን ባህሪ ስጫወት ሙሉ በሙሉ ሆኜ ለመጫወት ፍላጎት ስለነበረኝ፣ አደንዛዥ ዕፁን ተጠቅሜ፣ ራሴን ስቼ ደንዝዤ ነበር” ብሎ በጀብድ የተመላ ትርክቱን ነገረን፡፡
በዚህም ቢበቃን መልካም ነበረ…ደፋሩ ሰይፉሻም “እስኪ የፊልሙ ቅንጫቢ ከደረሰ ልቀቁልን” ብሎ አጋፋሪዎቹን አዘዘ፡፡ ወዲያው ግሩም አደንዛዥ ዕፁን ከወሰደ በኋላ የዕውነትም ደንዝዞ፣ ንፍጡ ተዝረክርኮና በላብ ተጠምቆ--- አንድ ጥግ ስር ተቀምጦ “ጦዣለሁ እኮ--” እያለ በመንተባተብ፣ ለሜካፕ ሰሪዎቹና ለካሜራ ባለሙያዎቹ ሲያወራ ፊልሙ ያሳያል፡፡ ይህ ትዕይንት ሲጠናቀቅ በዕለቱ የነበሩት ታዳሚዎች ለጀብደኛው ተዋናይ ግሩም፣ ከዕውቀት ፅድት ብለው ሲያጨበጭቡለት፣ ደፋሩ ሰይፉ ደግሞ ስለአደንዛዥ ዕፅ አስከፊነት ሊመካክረን ወደደ፡፡   
እንግዲህ የተከሰተው ይህ ነው፡፡ አደንዛዥ ዕፆችን አስመልክቶ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የወንጀል ህግ ምን እንደሚል ቃል በቃል የገለበጥኩትን ለአንባቢያን ላካፍል፡፡
የወንጀለኛ መቅጫ አንቀፅ 525
ማንኛውም ሰው ልዩ-ፈቃድ ሳይኖረው
ሀ. ዕፆችን ያበቀለ፣ ያመረተ፣ የሰራ፣ የለወጠ፤ ወይም የፈበረከ
ለ. ከላይ በፊደል (ሀ) ከተዘረዘሩት ነገሮች አንዱን ይዞ የተገኘ፣ ወደ አገር ያስገባ፣ ወደ ውጪ አገር የላከ፣ ያከማቸ፣ የደለለ፣ የገዛ፣ ያሰራጨ፣ ያዘዋወረ፣ አሳልፎ የሰጠ ወይም ለሌላ ያስገኘ
ሐ. ከላይ በፊደል (ሀ) ከተዘረዘሩት ነገሮች አንዱን ለማምረት፣ ለማቀነባበር፣ ወይም ለመፈብረክ የሚያገለግሉ መሳሪያዎችን የሰራ፣ ይዞ የተገኘ፣ ወደ አገር ውስጥ ያስገባ፣ ወይም ወደ ውጪ አገር የላከ
መ.  ከላይ በፊደል (ሀ) ለተዘረዘሩት ነገሮች መስሪያነት ማቀነባበሪያነት፣ ማምረቻነት፣ መሸጫነት፣ ወይም ባለይዞታ የሆነበትን ቤቱን፣ ግቢውን ወይም ቦታውን የሰጠ ቤቱን ያከራየ ወይም የፈቀደ እንደሆነ ከአምስት ዓመት በማያንስ ፅኑ እስራትና ከአንድ መቶ ሺህ ብር በማይበልጥ መቀጮ ይቀጣል፡፡
እንግዲህ ከዚህ አንቀፅ ብንነሳ በዋነኛነት ግሩም ከዚያም ገዝተው ያመጡት ዳይሬክተሮች፣ የፊልሙን መቅረጫ ቤት አከራዮች ወዘተ በሙሉ በወንጀል ሊጠየቁ የሚችሉበት ሁኔታ እንዳለ እንገነዘባለን፡፡ ከዚህም በላይ ደግሞ በዚሁ የወንጀለኛ መቅጫ ላይ የሚከተለውም ሰፍሮአል፡፡  
የወንጀለኛ መቅጫ አንቀፅ 640
ፀያፍ ወይም የብልግና ወይም ለመልካም ጠባይ ተቃራኒ የሆኑ ነገሮችን ለህዝብ መግለፅ
ማንኛውም ሰው  
ሀ. ፀያፍ ወይም ለመልካም ጠባይ ተቃራኒ የሆኑ የሆኑ ፅሁፎችን፣ ምስሎችን፣ ስዕላዊ መግለጫዎችን (ፖስተሮችን) ፊልሞችን ወይም ሌሎች ነገሮችን ያዘጋጀ፣ ወደ አገር ውስጥ ያስገባ፣ ወይም ወደ ውጪ አገር የላከ፣ የተቀበለ፣ የያዘ፣ ለህዝብ ያሳየ፣ ለሽያጭ ወይም ለኪራይ ያቀረበ፣ ያከፋፈለ፣ ያሰራጨ ወይም በማናቸውም ሌላመንገድ ከቦታ ቦታ ያዘዋወረ ወይም በእነዚህ ነገሮች የነገደ እንደሆነ የተከሰሰባቸው ነገሮች መወረሳቸው ወይም እንዲጠፉ መደረጋቸው ሳይቀር ከስድስት ወር በማያንስ ቀላል እስራትና በመቀጮ ይቀጣል…ይላል፡፡
እንግዲህ እዚህ ላይ ደግሞ እነ ኢቢኤስ፣ እነሰይፉሻ፣እነ የፊልሙ ፕሮዱዩሰሮችና የመሳሰሉት ከተጠያቂነት ላያመልጡ ነው፡፡ ስራውም ከመወረስ ላይድን የሚችልበት መንገድም አለ እንደማለት ነው።
ይህንን በዝርዝር ለመጥቀስ የተገደድኩት ሰይፉና መሰል የቶክ ሾውና የሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጆች--- ህዝብን እያዝናናን እናስተምራለን ከማለታቸው በፊት ለጥቂት ሰዓታትም ቢሆን ለንባብ ጊዜ እንዲመድቡ፣ የሚሰሩትንም  የህግ አግባብን በተከተለ መልኩ እንዲያደርጉት ለማሳሰብም ጭምር ነው፡፡
ኢቢኤስ ሃላፊነት እንዳለበት የሚዲያ ተቋም፣ ይህንን ፕሮግራም በዘፈቀደ ካስተላለፈ/ለዓየር ካበቃ በኋላ ደግሞ በከተማዋ የተሰሙትን ትችቶች መሰረት አድርጎ አቶ ሰይፉ በቅዳሜው የሸገር የአየር ሰዓቱ “ታዲያስ አዲስ” በተሰኘው ፕሮግራሙ ላይ ግሩምን በስልክ ጋብዞ ልክ ጀግንነት እንደሰራ ሰው ሲወዳደሱ ስሰማ፣ ብስጭቴን ለመቆጣጠር ተስኖኛል፡፡ ቃል በቃል ባላስታውሰውም አንድ ሶስት የተባባሉትን ሃሳቦች ላካፍላችሁ፡፡
ሰይፉ፤- እኛ ትምህርት እናስተምራለን ብለን ነበር  ያቀረብነው…ግሩሜ ያንን በመስራትህ ትፀፀታለህ?
ግሩም፤- በፍፁም አልፀፀትም፡፡ እኔ እንደውም ከህዝቡ የተለየ አድናቆትና ሽልማት ነበር ስጠብቅ የነበረው፡፡ በዚህ በጣም ስሜቴ ተነክቶአል፡፡
ሰይፉ፤- አንዳንድ ሰዎች “ሆኖ መጫወት” ትንሽ ይከብዳል ይላሉ…ለምሳሌ አፄ ቴዎድሮስን ሆኖ ቢሰራ ጥይቱን የዕውነት ሊጠጣ ነው? እያሉ ነው፣ ምን ትላለህ? (አያችሁ መልሶ ሲያሾፍበት…የእርሱኑ ፕሮግራም ባደመቀ!)
ግሩም፡- ይህንን የሚሉት ፍልስፍናው ስላልገባቸው ነው፡፡ ቢገባቸው እንዲህ አይሉም፡፡ መሆን ሲባል ሁሉም ነገር አይኮንም…ለምሳሌ ሞት፣ እሳት መቃጠል ወዘተ-- ተሆኖ ሊተወን አይችልም
ሰይፉ፤- እና ይቅርታ አትጠይቅም?
ግሩም፤- እኔ ምናልባት ይቅርታ መጠየቅ ካለብኝም ከ18 ዓመት በታች የሆኑትን ህፃናት ነው። እነሱን አስቀይሜ ከሆነ ይቅርታ እጠይቃቸዋለሁ፡፡ በሌላው ግን ለማስተማር ስለሆነ የሰራሁት ልደነቅ እንጂ እንዲህ ስሜቴ ሊነካ አይገባም ወዘተ--
እንዲህ እንዲህ ተባብለው ስልኩ ተዘጋ፡፡ ወዳጆቼ… ይቅርታ መጠየቅ ብቻም ሳይሆን በህግም መጠየቅ አለ እያልን እኮ ነው፡፡ ይህንን እየፃፍኩ አንድ ሁልጊዜ የሚከነክነኝና የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የልጆችና የወጣቶች ፕሮግራም አዘጋጅ ሆኜ የተከሰተ አንድ ክስተትን አስታወስኩ፡፡
የአባባ ተስፋዬ ከኢቴቪ መባረር!
 እንደምታስታውሱት ባንድ ወቅት በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የልጆች ፕሮግራም ላይ የኦሮሞ ብሄረሰብን ክብር የሚነካ ቃል በአንዲት ህፃን በተረት መልክ ተነግሮ ብዙ አዳርሶ ነበር፡፡ በወቅቱ የነበሩት የጣቢያው የበላይ ሃላፊዎች አባባ ተስፋዬንና የእለቱ ፕሮግራም አስፈፃሚ የነበረችውን ባልደረባችንን ከስራ ሲያግዱ፣ በጣቢያው የሁለት ሰዓቱ የዜና እወጃ ላይ፣ መላውን የኦሮሞ ህዝብ በይፋ በጣቢያው ስም ይቅርታ ጠይቀዋል፡፡ ይህ የይቅርታ ጥያቄ ተገቢና የሰለጠነ አካሄድም እንደነበረ ተገንዝቤአለሁ፡፡ የህዝብን ክብር የሚነካ፤ የሚያሳቅቅና የሚያሸማቅቅ ተግባር በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ሲፈፀም ጣቢያው የመጀመሪያውን ሃላፊነት ወስዶ ይቅርታ መጠየቅ በእርግጥም መሰልጠን ነው፡፡ እንደነ ሰይፉ ዓይነቱ ደፋር ደግሞ በኢቢኤስ ላይ የሰራውን ስህተት በሸገር ሬዲዮ ላይ ይጨማምርበታል፡፡
ሰይፉ በተለያዩ ጊዜያት ባለሙያዎች ላይ ሲያፌዝ፣ ሲያንጉዋጥጣቸው፣ በአራዶቹ አነጋገር ሙድ ሲይዝባቸው አድምጨዋለሁ፡፡ እንደ ሳያት ያለችዋ ጀግና ደግሞ ሰጥ-ለጥ ስታደርገውም አስታውሳለሁ፡፡ በይፋም ይቅርታ አስጠይቃው እንደነበር ይታወሳል፡፡ ሆኖም በዕንቁላሉ ጊዜ ተገቢው እርምጃ ያልተወሰደበት ሰይፉ ፋንታሁን፣ ነገ ደግሞ ምን እንደሚያመጣብን ምን ይታወቃል?
እዚህ ላይ አንድ ሸዋፈራሁ ደሳለኝ የሚሰራት ማስታወቂያ ትዝ አለኝ፡፡ ማስታወቂያው የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ባለስልጣን መልዕክትን ለማስተላለፍ የተዘጋጀ ነው፡፡
በአንድ የሬዴዮ ጣቢያ የተላለፈ ዘገባ፣ የድርጅቴን ስምና ክብር አጉድፏል ብሎ ሸዋፈራሁ በወከላቸው ሽማግሌ ገፀ-ባህሪ አማካኝነት ለብሮድካስቱ ባለስልጣን ክስ ሊያቀርብ ሲንቀሳቀስ ያሳይና እንዲህ ዓይነቱ የመብት ጥሰትና መሰል አግባብ ያልሆኑ ነገሮች ሲተላለፉ አቤት ማለት እንደሚቻል ያስተዋውቃል፡፡
እና እኛም (እኔና እኔን መሰሎች) እንደ ትውልድ ተቆርቋሪ - ኢቢኤስ ቲቪ፣ ሰይፉ ፋንታሁንና ግሩም ኤርሚያስ በጋራ ሆነው ይቅርታ ካልጠየቁን የሸዋፈራሁን ጥቆማ ተግባራዊ የምናደርግበት ቀን ሩቅ ላይሆን ይችላል፡፡
መልካም በዓል!

Published in ባህል

ኒዮሊበራሎች ያሴሩት “የቀለም አብዮት” ቦሌ ኤርፖርት ከሸፈ  
የቀለም አብዮት ፍቱን መድሃኒት- የህዝብ ፍቅር ነው!
ሰኞ እለት ምሽት ይመስለኛል። እቃ ለመሸመት ወደ አንድ ሱቅ ጎራ ብዬ ሳለሁ ነው የሰማሁት - የሬዲዮ የቀጥታ የስልክ ውይይቱን። በየትኛው ጣቢያ እንደነበር ግን አላወቅሁም። ደዋይዋ  ተማሪ ናት። ከጋዜጠኛዋ ጋር ሰላምታ ከተለዋወጡ በኋላ፣ ሰፈራቸው ውሃ ጠፍቶ በጣም እንደደበራት በምሬት  ተናገረች - ተማሪዋ። ጋዜጠኛዋ የውሃው መጥፋት የተከሰተው እየተከናወነ ባለው የልማት ሥራ የተነሳ በመሆኑ ብዙም  ልትማረር እንደማይገባት  አስረግጣ ነገረቻት። (የእድገት ምስቅልቅል ነው ማለቷ እኮ ነው!) ደዋይዋ ግን የጋዜጠኛዋ መልስ  የተዋጠላት አትመስልም። “ኮብልስቶን ሲሰሩ እኮ ነው ---” ስትል አከለችላት። (“አውቀው ነው እንጂ “ውሃችን ሳትጠፋ ኮብልስቶኑን መስራት ያቅታቸዋል?!” የሚል ሃሳብ ውስጧ የቀረ ይመስላል)  
 ጋዜጠኛዋ በፍጥነት መለሰችላት “እንደውም ሰምተሽ ከሆነ --- አገራችን በኮብልስቶን  ዓለም አቀፍ ሽልማት አግኝታለች ----እና ለልማት የሚከፈል መስዋዕትነት ነው”  
“ቢሆንም  ይሄ እኮ መሠረታዊ ፍላጎት ነው” አለቻት ተማሪዋ ድምጿን መረር አድርጋ።
“ መሠረታዊ ፍላጎት ቢሆንም ለልማት ሲባል አንድ ሁለት ቀን ብትታገሽ ምንም አይደለም --- አየሽ እኛ መስዋዕትነት ከፍለን ለመጪው ትውልድ ያደገች አገር ማስረከብ አለብን”   
“እኛንም ይመለከታል  ማለት ነው?” ጠየቀች ደዋይዋ ተማሪ። (“መስዋዕትነቱ ለኛ አይደለም ወይ?” የምትል ትመስላለች!)
“እየቀለድሽ ነው አይደል---እናንተ ኢትዮጵያውያን አይደላችሁም  እንዴ? ይሄ እኮ  ሁሉንም ኢትዮጵያዊ የሚመለከት ጉዳይ  ነው” በመገረም በተሞላ ቅላፄ መለሰችላት።
ከደዋይዋ ድምፀት እንደተረዳሁት የጋዜጠኛዋ ምላሽ ያረካት አትመስልም። ለነገሩ እንኳን ታዳጊዋን  እኔንም አላረካኝም። አረ እንደውም አናዶኛል። (“ልማት ላይ ስለሆንን አንድ ሁለት ቀን ውሃ ባትጠጪ ምን ትሆኛለሽ” ማለት እኮ ነው የቀራት!) በነገራችሁ ይሄ “ልማት” ---- ለብዙ ዳተኞች ተመችቷቸዋል። (የሆነውንም ያልሆነውንም በልማቱ እያሳበቡ ለሽ ይላሉ!)
እስቲ አሁን ደሞ ከሬዲዮ ወጥተን ወደ ቴሌቪዥን እንግባ።  
  ባለፈው ሳምንት ኢቴቪ “የቀለም አብዮት ሰለባዎች” በሚል ርዕስ የተዘጋጀ  ዶክመንታሪ በቅዳሜ ምሽት ፕሮግራሙ እንደሚያቀርብ ደጋግሞ ሲያስተዋውቅ፣ አንድ ለየት ያለ መረጃ ወይም ፍንጭ እጁ እንደገባ እርግጠኛ ነበርኩ። ለምን መሰላችሁ? ኢቴቪ ከመሬት ተነስቶ  ዶክመንተሪ አይሰራማ። አንድም ለማጋለጥ ነው አሊያም ለማስጠንቀቅ። (በ“አንድነት” ላይ ያነጣጠረው አኬልዳማ  ትዝ አይላችሁም?) በነገራችሁ ላይ---ኢቴቪ  በአኬልዳማ  ሳቢያ  ፈፅሞ ያላሰበው ጣጣ ውስጥ ገብቷል። አንድነት የተባለ ተቃዋሚ  ፓርቲ፣ በስም ማጥፋት ወንጀል ፍርድ ቤት ይገትረኛል ብሎ አስቦም አልሞም አያውቅም። (ህጉን አያውቅም  እንዴ?) ከተከሰሰም በኋላ  ቢሆን  ይፈረድብኛል ብሎ አላሰበም። ለምን መሰላችሁ ? ራሱን እንደ “ንጉስ” ነበር የሚቆጥረዋ (“ንጉስ አይከሰስ ሠማይ አይታረስ አሉ!”)
ኢቴቪን በቅርብ የሚያውቁት እንደሚናገሩት፤ ይሄን የመታበይ ስሜት ለመጀመርያ ጊዜ የፈጠሩበት ንጉሱ ናቸው። በደርግም ንጉስ በሌለበት እንደንጉስ ያደርገው ነበር -ኢቴቪ። ብቻ የአገሪቱ መንግስታት ሁሉ   እንደ አያት አቅብጠው ነው ያሳደጉት! ዘንድሮ ግን ከባድ ፈተና ገጠመው። በአንድነት የተከሰሰው ኢቴቪ፤ ስምና ክብር አጉድፈሃል ተብሎ የጎደፈውን ስምና ክብር የሚመልስ ማስተባበያ እንዲያስተናግድ በፍርድ ቤት ተወስኗል። ምንም እንኳን ይግባኝ እጠይቃለሁ ቢልም። እርግጠኛ ነኝ ከዚህ በኋላ ያለአስተማማኝ መረጃ የሰው ስም አያጠፋም። (The hard way እኮ ነው የተማረው!) መቼም ኢህአዴግም ይሁን መንግስት የሰው ስምና ክብር እንዲያጎድፍ አያስቸግሩትም። (ቢያስቸግሩትም በጄ ማለት የለበትም!)   
 እናላችሁ ---ቅዳሜ ደርሶ “የቀለም አብዮት ሰለባዎች” የተሰኘውን ዶክመንታሪ ለማየት ቸኩዬም ጓጉቼም ነበር። እንደማይደርስ የለም ቀኑ ደረሰ፤ እንደጠበቅሁት ግን  አልነበረም። (አይረባም አልወጣኝም!) ከዚህ በፊት የማይታወቅ ምስጢር ወይም ፍንጭ አልሰጠኝም ማለቴ ነው። በእርግጥ ለብዙዎች ስለቀለም አብዮት አፈጣጠርና ምንነት ደህና ግንዛቤ ያስጨብጣል። እናንተ---ይሄ የቀለም አብዮት ቀላል ኢንቨስትመንት መሰላችሁ! የቢሊዮን  ዶላር ፕሮጀክት እኮ ነው። አሜሪካ በዩክሬን ለተካሄደው ብርቱካናማው አብዮት ስንት እንደመደበች ታውቃላችሁ? 5 ቢሊዮን  ዶላር! (ለአንድ አብዮት ብቻ?)
        የቀለም አብዮት ላይ ያነጣጠረው ዶክመንታሪ፤ በአብዛኛው በቀለም አብዮት እየተቀጣጠለች ባለችው ዩክሬን ላይ የሚያተኩር ሲሆን በሦስት ባለሙያዎች አስተያየት ተደግፎ የቀረበ ነው። “የቀለም አብዮት ተንታኞች” ብያቸዋለሁ። እኔ የምላችሁ----- ይሄ የቀለም አብዮት ስንት ስም ነው ያለው! በነገራችሁ ላይ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ  (ነፍሳቸውን ይማረውና!) ብርቱካናማውን አብዮት “የአትክልትና ፍራፍሬ አብዮት” ሲሉ ተሳልቀውበት ነበር። እንዲያም ሆኖ ግን የዩክሬንን ብርቱካናማ አብዮት ለመድገም አስበዋል የተባሉትን ተቃዋሚ ፓርቲዎች “ብትሞክሯት ውርድ ከራሴ በሉ” እንዳሏቸው ምንጮች  ይጠቁማሉ።
“የቀለም አብዮት” ሰለባዎች በሚለው ዶክመንተሪ ላይ  አስተያየት የሰጡት ተንታኞች እንደሚሉት፣ ምዕራባውያን በ97 ምርጫ  በጦቢያችን  ላይ የቀለም  አብዮት የማቀጣጠል እቅድ የነበራቸው ቢሆንም አልተሳካላቸውም።
እስካሁን በዓለም የተለያዩ አገራት በርካታ  የቀለም አብዮቶች መካሄዳቸውን  ያወሱት ተንታኞቹ፤ የምዕራባውያኑ ዓላማ አልታዘዝ ያሏቸውን መንግስታት በህዝባዊ አመፅ ከሥልጣን በማውረድ  ርዕዮተ ዓለማቸውን የሚያስከብርላቸውን  የትሮይ ፈረስ ቤተመንግስት ማስገባት  ነው ብለዋል። የቀለም አብዮት የማይሳካበት አገር ብቸኛዋ  ቬኔዝዌላ እንደሆነች የገለፁት አንዱ ተንታኝ ፤ እ.ኤ.አ ከ1999 ጀምሮ አገሪቱን የመሩት ሁጎ ቻቬዝ በህዝብ ዘንድ ተወዳጅ ስለነበሩ በቀለም አብዮት ከሥልጣን እንዲወርዱ ቢደረግም ህዝቡ አብዮቱን በማክሸፍ ወደ ሥልጣን መልሷቸዋል ብሏል። (የቀለም አብዮት ፍቱን መድሃኒት- የህዝብ ፍቅር ነው!)
ምዕራባውያን ኢትዮጵያን በቀለም አብዮት ለማፈራረስ ይሞክሩ  ይሆን? በሚል ለቀረበው ጥያቄ ተንታኞቹ  ሁለት የተለያዩ ምላሾች ሰጥተዋል። ሊሞክሩ ይችላሉና አይሞክሩም በሚል። ኢትዮጵያ ከምዕራባውያን ጋር በሚያስማሟት ጉዳዮች ላይ ተባብራ  እየሰራች መሆኑን የገለፁት ተንታኙ፤አገሪቱን በቀለም አብዮት ለማፈራረስ  የሚፈልጉበት ምክንያት የለም ይላሉ። ምዕራባውያን የማይፈልጓቸውን መንግስታት የሚቀጡት የልማት እርዳታ  በመከልከል መሆኑን በመጠቆምም፤ በእኛ አገር ሁኔታ ግን የልማት እርዳታ  በየጊዜው እየጨመረ መምጣቱን ገልፀዋል። (“ብሩህ ተስፈኛ” ብያቸዋለሁ!)  ሌላኛው የቀለም አብዮት ተንታኝ በበኩላቸው፤ ምእራባውያኑ በጦቢያ ላይ የቀለም አብዮት ሊያቀጣጥሉ ይችላሉ ባይ ናቸው። ለዚህ ዋና ሰበቡም የርዕዮተ ዓለም ልዩነት መሆኑን ይናገራሉ። ኢህአዴግ መራሹ መንግስት አስፈላጊ በሆኑ የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ ጣልቃ መግባት ይፈልጋል (ቁጭ ብሎማ አይመለከትም!) ምዕራባውያኑ ግን  መንግስት ሁሉን ነገር ለውጭ ኢንቨስተር ክፍት እንዲያደርግ ነው የሚፈልጉት።  (የግል ባለሃብት መጫወቻ ሊያደርጉት እኮ ነው!) ይሄ ቅራኔ ብቻ ነው ለቀለም አብዮት መሠረታዊ ምክንያት የሚሆነው ብለዋል -ተንታኙ። በተረፈ ግን ሁሉም ሙሉ ሁሉም ዝግጁ ስለሆነ ጦቢያን የቀለም አብዮት አያሰጋትም  ባይ ናቸው።
ከዚሁ ከቀለም አብዮት ሳንወጣ ባሳለፍነው ሳምንት በኢቴቪ የሰማሁትን አንድ አስደንጋጭ ዜና ልንገራችሁ - ላልሰማችሁ። ከሦስቱ አንጋፋ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ማህበራት የአንዱ ፕሬዚዳንት ለኢቴቪ እንደተናገሩት፤ የቀለም አብዮት ለማቀጣጠል የመጡ አርቲክል 19 የተባለ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት ተወካይ ወደ አገር ውስጥ ሳይገቡ እንዲመለሱ ተደርገዋል - ከቦሌ አየር ማረፍያ። ተወካዩ ወደ ኢትዮጵያ የመጡት ለጋዜጠኞች ሥልጠና ለመስጠት እንደነበር ውስጥ አዋቂ ምንጮች  ቢናገሩም፣ የጋዜጠኛ ማህበሩ ፕሬዚዳንት ግን  በዚህ አይስማሙም። ሰውየውም ሰልጣኞቹም  ህገወጥ ናቸው ብለዋል- ፕሬዚዳንቱ። እናም  በኒዮሊበራሎች  የታቀደው “የቀለም አብዮት” ቦሌ አየር ማረፍያ ላይ ከሽፏል።
 እኔ የምለው ግን ----የቀለም አብዮት ትፈራላችሁ እንዴ? (ይሄማ የጦቢያን ልጆች ታሪክ መርሳት ነው!)  እንኳንስ ለቀለም አብዮተኞች ለፋሺስት ኢጣልያም እጅ አልሰጠንም እኮ! አያችሁ ---- ኢህአዴግም ሆነ   መንግስት መፍራት ያለባቸው ህዝብን እንጂ የቀለም አብዮተኞችን አይደለም።
ሥልጣን የሚሰጥም የሚነሳም ህዝብ  ነው! (የ97ቱን ምርጫ ልብ ይሏል!) እናም  ህዝብ የሚወደው መንግስት የቀለምም ይሁን የፍራፍሬ አብዮት ጨርሶ አያስፈራውም (“ህዝብ የሚወደው መንግስት” እንዴት ያለ ነው?) እናላችሁ----ኢህአዴግ ነፍሴ ከመስጋት ይልቅ ብልህ መሆን ነው የሚያዋጣው። ከልማት ሥራው ጎን ለጎን በመብራት፣ በውሃ፣ በኔትዎርክ፣ በትራንስፖርት፣ በዳቦ ወዘተ-- እጥረትና መጥፋት ለሚሰቃየው ህዝብ፤ዛሬ ነገ ሳይል አፋጣኝ መፍትሄ ይዘይድ።
መንገዱ ወጣ ገባና ኮረኮንች ቢበዛውም “አገር ውስጥ ሰላማዊ ትግል ማካሄድ ይቻላል” ብለው በህጋዊነት  የሚንቀሳቀሱ  ተቃዋሚዎችን አትላወሱም ብሎ ማዋከብ፣ትርፉ የጠላትን ቁጥር ማብዛት ብቻ  ነው።  እናም በዶክመንታሪው ላይ አንዱ ተንታኝ እንዳሉት፣ የቀለም አብዮትን ለመከላከል የቤት ሥራን አጥርቶ መስራት የግድ ይላል።
መልካም የትንሳኤ በዓል ይሁንላችሁ!! 

       ለአስራ ሰባት አመታት የዘለቀ እጅግ መራራና ፈታኝ የትጥቅ ትግል በማካሄድ ደርግን የገረሰሰው ኢህአዴግ፤እነሆ ላለፉት 23 ዓመታት ስልጣንን ተቆጣጥሮ ሀገሪቱን በመምራት ላይ ይገኛል። ኢህአዴግ ስልጣን ላይ ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ በርካታ ፖለቲካዊ፣ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ተከናውነዋል። በፖለቲካው መስክ በተለይም የህዝቦችን ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች በተመለከተ ከተከናወኑት ድርጊቶች ውስጥ ለእነዚህ መብቶች መከበር ህጋዊ ዋስትና ያጐናፀፋቸው ህገመንግስት ፀድቆ፣ወደ ተግባር መገባቱ አንዱና ምናልባትም ዋነኛው ክንውን ይመስለኛል።
ዲሞክራሲ ለሀገራችን የቅንጦት ወይም የምርጫ ጉዳይ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ መሆኑን ኢህአዴግ ላለፉት በርካታ አመታት እስኪሰለቸን ድረስ ነግሮናል። በተለይ ደግሞ የህገመንግስቱ ነገር እንዲሁ እንደተራ ጉዳይ የሚታይ ሳይሆን ማንም ቢሆን ልክ እንደታቦት ሊያከብረውና ሊያስከብረው የሚገባ ጉዳይ መሆኑን አበክሮ ሲያሳስበን ኖሯል። ኢህአዴግ ይህንን ማድረጉ አያስወቅሰውም። እንደውም ያስመሰግነዋል እንጂ። ችግሩ የሚመጣው “ኢህአዴግ የሚሰብከውን በተግባር ይፈፅማል ወይ?” ብለን ስንጠይቅ ነው።
በሀገራችን እየተካሄደ ያለውን የዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ በተመለከተ ኢህአዴግ ላለፉት 23 ዓመታት ራሱን የሂደቱ ዋና ሻምፒዮን አድርጎ ሲቆጥርና እኛም እንድንቆጥርለት ሲታትር ነው የኖረው። በእርግጥ በዚህ ጉዳይ ላይ በግንባር ቀደምትነት ከሚሰለፉት ኃይሎች አንዱ መሆኑን ማንም ሊክደው አይችልም። ይሁን እንጂ ኢህአዴግ በዚህ እውቅና የማግኘት የማራቶን ሩጫው፣መሰረታዊውንና ዋነኛውን ቁልፍ ጉዳይ አውቆም ይሁን ሳያውቅ የዘነጋው ይመስላል። ብሔራዊ ስልጣን ጨብጠው ህዝብንና ሀገርን የመምራት ታሪካዊ ኃላፊነትን የተሸከሙ መንግስታት፣ በህዝብ ዘንድ የሚኖራቸው እውቅናም ሆነ በታሪክ ማህደር የሚይዙት ሥፍራ የሚወሰነው እወቁኝ ወይም እወቁልኝ በሚል ውትወታ አልያም ሳይታክቱ በሚያደርጉት ሰበካ ሳይሆን በተግባር በሚያከናውኑት ድርጊት ብቻ መሆኑን ኢህአዴግ በእርግጥም አላጤነውም።
ህገ መንግስታዊ እውቅና ያገኙትን የህዝቦች ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች በማስጠበቅና በመጠበቁ በኩል ኢህአዴግ ላለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ሲነግረን የኖረው በተግባር ከሚፈጽመው ድርጊት ጋር ጨርሶ የሚጣጣም አይደለም። ይህ ተራ ስሞታ ወይም መሰረተ ቢስ ውንጀላ እንዳልሆነ ኢህአዴግ ራሱ ያምናል። እርግጥ ነው በየትም አገር ቢሆን የዲሞክራሲ ስርአት በአንድ ጀምበር አልተገነባም። አይገነባምም። ለዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ ደግሞ የህግ የበላይነት መረጋገጥ ቁልፍ ጉዳይ መሆኑን አንስተውም። የህግ የበላይነት እንዲረጋገጥ፣የሀገሪቱ ህጎች በሁሉም ዘንድ መከበርና መጠበቅ አለባቸው። በዚህ ረገድ ከማንም በላይ የግንዛቤ ክፍተት የሚታይበት ቀን ተሌት የህግ የበላይነትን የሚሰብከው ራሱ ኢህአዴግ ነው ብንል አልዋሸንም። ዛሬ በመላው የሃገሪቱ ክልል የህዝቦች አይነኬ ሰብአዊ መብቶች ከህግ አግባብ ውጭ የሚጣሱትና የሚረገጡት በዋናነት በመንግስት አካላት ነው። ህገመንግስታዊ ዋስትና የተሰጣቸው የህዝቦች በነፃ የመደራጀት፣ በነፃ የመሰብሰብ፣ በነፃ ሀሳብን የመግለጽ፣ የፕሬስ ነፃነትና የመሳሰሉት  የዲሞክራሲ መብቶች በዋናነት ኢህአዴግ በሚመራቸው የመንግስት አካላት ይጣሳሉ። ይሄ የሀሰት ስሞታ አለመሆኑን ለማረጋገጥ ደግሞ ከራሱ ከኢህአዴግ ሌላ እማኝ መጥቀስ ፈጽሞ አያስፈልገኝም። ኢህአዴግ ስር የሰደደ የመልካም አስተዳደር ችግሮች እንዳሉበት ያልነገረን ጊዜ የለም።
ለዚህ ስር የሰደደ የመልካም አስተዳደር ችግር ሁለት ዋና ዋና ጉዳዮችን እንደ መሠረታዊ መንስኤ ማቅረብ እንችላለን። አንደኛው ጉዳይ ኢህአዴግ እንደ ገዢ ፓርቲነቱ የራሱን ሚና ህግ በማውጣትና በማስፈፀም ብቻ ወስኖ፣ህግን ማክበር የሌሎች ሃላፊነት እንደሆነ አምኖ መቀበሉ ይመስለኛል። ሁለተኛው መሠረታዊ ነጥብ ደግሞ ራሱን ከህግ በላይ አድርጐ መቁጠሩና ህግን የመጠበቅ ሃላፊነት እንዳለበት በአስገራሚ ሁኔታ መርሳቱ ነው።
 ህገመንግስቱ የህጐች ሁሉ የበላይ ህግ መሆኑንና እሱን መጣስ ማለት ታቦት እንደ መርገጥ እንደሚቆጠር ወደን እስክንጠላ ድረስ ቢሰብከንም ለራሱ ግን አይጠቀምበትም። ምናልባትም እሱን የሚመለከተው አይመስለውም። ምንም እንኳን ኢህአዴግ የሰው ምክርና ሃሳብ የመቀበል በጎ ልማድ ባያዳብርም እኛ ግን ሁሌም ሳንሰለች መወትወታችን አልቀረም። እስከዛሬ ግን ጆሮ ዳባ ልበስ እንዳለን ነው። አሁንም ግን አንሰለችም። አንድ ቀን ጆሮ ይሰጠናል በሚል ተስፋ፣ ስጋታችንንና ጭንቀታችንን መተንፈሳችን ይቀጥላል። እናም ከዚህ ቀደም እንደምክር የነገርነውን አሁን ደግሞ በተማፅኖ እንጠይቀዋለን “ኢህአዴግ ሆይ፤እንደው በምታምነው ታቦት ይዘንሃል ---- እባክህን ጠብቃችሁ አስጠብቁት የምትለንን ህገመንግስት አንተም አክብረው፣አንተም ጠብቀው” በማለት። እርግጥ ነው በተለያዩ የልማት ሥራዎች ተጠምዷል። ነገር ግን በልማት ሥራ መጠመድ ህገመንግስቱን ከማክበርና ከማስከበር አያግድም። እናም በድጋሚ “የተከበርክ ኢህአዴግ፣ እባክህ ስለ ፈጣሪ ብለህ ህገመንግስቱን አክብርልን!” እንለዋለን።
ኢህአዴግ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ያላቸውን ሚና በተመለከተ ሲገልፅ፤“ለሀገራችን የዲሞክራሲ ግንባታና ዴሞክራሲያዊ ባህል መዳበር ጠንካራና ህዝባዊ መሰረት ያላቸው የተቃዋሚ ፓርቲዎች መኖር በእጅጉ አስፈላጊ ነው። ስለዚህ የተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዲፈጠሩ መፈለግ ብቻ ሳይሆን እንዲፈጠሩ ለማድረግም የድርሻዬን እወጣለሁ” ብሎ ነበር - ያውም በአደባባይ። ኢህአዴግ ይህን ኮሚክ የሆነ የፖለቲካ ጨዋታ ሲያስብ “ዓለም መጭበርበርን ትወዳለች” የሚለው የሆላንዳዊያን የተለመደ አነጋገር ትዝ ሳይለው አይቀርም። ኢህአዴግ ጨርሶ ያልተረዳው ነገር ቢኖር፣ እኛ አረፋው ሁሉ ቢራ አለመሆኑን በሚገባ ማወቃችንን ነው። ላለፉት 23 ዓመታት በዓይናችን እንዳየነው፣ ጠንካራ የተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዲፈጠሩ መፈለጉን የሚጠቁም አንዳችም የረባ ጥረት አላደረገም። እንደውም ያሉት እንዲከስሙ የበለጠ ተንቀሳቅሷል ቢባል ይሻላል።
የመጀመርያውን ቃሉን ያልፈፀመው ኢህአዴግ፣ የማታ ማታ ከተጠያቂነት ለማምለጥ ሲል “እንደአለመታደል ሆኖ ጠንካራ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ሊፈጠሩ ባለመቻላቸው ኢህአዴግ የአውራ ፓርቲነትን ከባድ ቀንበር ለመሸከም ተገዷል” አለን። በአንድ ወገን ስትመለከቱት እውነቱን ነው ያስብላል። በአባላት ብዛት፣ በቢሮና መሰል ተቋማት ጥንካሬ እንዲሁም በገንዘብ አቅም ከታየ፣ በእርግጥም ኢህዴግ አውራ ፓርቲ ነው። በዚህች አገር ላይ እንኳንስ የሚፎካከረው አጠገቡ ድርሽ የሚል አንድም የተቃዋሚ ፓርቲ አስሶ ማግኘት አይቻልም። ግን ኢህአዴግ የሚፈፅማቸው አንዳንድ ድርጊቶች እንኳንስ ከአውራ ፓርቲ ከተራ ፓርቲም የሚጠበቅ አይደለም። ከሰባት ሚሊዮን በላይ አባላት ያሉት፣ በየክልሎቹ ግዙፍ የቢሮ ህንፃዎችና ፈርጣማ የገንዘብ ጡንቻ ባለቤት የሆነው ኢህአዴግ፤ እንኳን ሊፎካከሩት ቀርቶ አይኑ ውስጥ ቢገቡም የማይቆረቁሩት የተቃዋሚ ፓርቲዎች የኪራይ ቢሮ እንዳያገኙ፣ የስብሰባ አዳራሽ እንዳይከራዩ፣ ህዝባዊ ስብሰባም ሆነ ቅስቀሳ እንዳያደርጉ፣ አባላትን በነፃነት እንዳይመለምሉ ---- እንቅፋት መፍጠሩ ከአውራ ፓርቲነት ያሳንሰዋል። እውነቱን ለመናገር ግን እንዲህ ያለ የሰፈር ጉልቤ ዓይነት የወረደ ተግባር ራሱን አውራ ነኝ ከሚል ፓርቲ ጨርሶ አይጠበቅም። የአውራ ፓርቲነት ከባድ እዳ ለመሸከም ተገድጃለሁ እያለ ዘወትር የሚነግረን ኢህአዴግ፤የአንድ እጅ ጣት የማይሞሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትን ከህግ አግባብ ውጪ ስብሰባ እንዳያካሂዱ በእስር ማዋከብና የሞባይል ስልካቸውን ኬሚካል ውስጥ መንከርን የመሰለ እጅግ አስነዋሪ ድርጊት መፈፀሙ እንኳን ለሌላው ለደጋፊዎቹም ሃፍረት መፍጠሩ አይቀርም። ወደፊት አገሪቱን ለሚረከቡት የአዲስ ትውልድ አባላትም መጥፎ አርአያ መሆኑ አያከራክርም። ኢህአዴግ መቼ ይሆን “ምራቁን እንደዋጠ ፓርቲ” ማሰብና መንቀሳቀስ የሚጀምረው? ያቺ ቀን ትናፍቀኛለች።


አንዳንድ በጣም ቀላል ተረት ሲቆይ እጅግ ትልቅ ታሪክ ይመስላል።
ከዕለታት አንድ ቀን የትልቅ አገርና የትንሽ አገር ሁለት ሰዎች ይገናኛሉ። ከዚያም አንድ የዓመት በዓል ዕንቁላል ሰብሮ አስኳሉን ለማውጣት በየት በኩል ቢሰበር ይሻላል የሚል ጥያቄ ያነሳሉ።
ከትንሽ አገር የመጡት አዛውንት፤ “ዕንቁላሉን ከጎን ሞላልኛ ጫፉ ላይ ብንመታው ነው አስኳሉ ሙሉውን ከነውሃው የሚወጣው” አሉ። ከትልቅ አገር የመጡት አዛውንት ደሞ፤ “የለም ወገቡ ላይ ብንመታው ነው ሙሉውን አስኳል ከነውሃው የምናገኘው” አሉ።
ቀኑን ሙሉ “አይሆንም ይሆናል”፣ “ልክ ነህ፣ ልክ አይደለህም፣” ሲባባሉ ዋሉ።
“አይ የትልቅ አገር ሰው በጣም ያሳዝናል! ዕንቁላል እንኳን መስበር አይችልም” አሉ የትንሽ አገር ሰው።
“የትንሽ አገር ሰው ፈፅሞ አይረባም። ዕንቁላል እንዴት እንደሚሰበር እንኳን የማያውቅ መሀይም ነው” አሉ የትልቅ አገር ሰው።
ተካረሩ፡፤ ተማረሩ!
“ይሄን ካልክ ሁለተኛ ዐይንህን አላይም። ለልጆቼም የትልቅ አገር ሰዎች ምን ዓይነት አላዋቂዎች እንደሆናችሁ እነግራቸዋለሁ!” አሉ አንደኛው።
“አንተም መቃብሬ ጋ እንዳትደርስ! እኔም መቃብርህ ጋ አልደርስም!” አሉ ሌላኛው።
እየተሰዳደቡ እኚህም ወደ ትልቅ አገር፣ እኒያም ወደ ትንሽ አገር ሄዱ። ብዙ ጊዜ አለፋቸው። ጉዳዩ የታሪክ ያህል አረጀ። ዋለ አደረና፤ በማናቸውም አጋጣሚ የትልቅ አገር ልጅ ወደ ትንሽ አገር ከሄደ ተደብድቦ ይመለሳል። በሌላ አጋጣሚ የትንሽ አገር ልጅ ወደ ትልቅ አገር ከሄደ ዱላ ቀምሶ ይመለሳል።
ነገር እየገፋ ሲሄድ የትልቅ አገርና የትንሽ አገር ሰዎች ጠላቶች ነን ተባባሉ። ጠበኝነታቸው በልጆች መደብደብ የሚያባራ አልሆነም። ወደ ጦርነት ገቡ። ሰው ተላለቀ። ብዙ ሬሣ ወደያገራቸው አጋዙ። ጦርነቱና ዕልቂቱ የማይቆም ሲመስል የጎረቤት አገሮች ጣልቃ ገብተው አገላገሏቸው። ሽምግልናም ተቀመጡ። በታሪክ በጣም ወደ ኋላ ሄደው ነገሩ ሲጣራ፣ ለካ “ዕንቁላል በየት በኩል ነው መሰበር ያለበት?” በሚል ነው ቅድመ - አያቶቻቸው ሲከራከሩ የተጣሉት። ለጊዜው ታረቁ።
የዛሬዎቹ የልጅ-ልጆች ግን፤ “ከአባቶቻችንና ከአያቶቻችን ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ ጠብና ጠላትነት አለን!” ይላሉ። ዛሬም።
*      *       *
ጉዳይን በጥሞና መርምረን ሀቁ ጋ መድረስ እያቃተን ጭራና ቀንድ ቀጥለን፣ አካብደን፣ አከባብደን ስንከራከርበት አሣር የሚያህል ፖለቲካ፣ አሣር የሚያህል የፓርቲዎች ግጭት፣ አሣር የሚያህል የመንግሥታት ውዝግብና ጦርነት ጋ እንደርሳለን። ከዚያም ለልጅ ልጅ የሚደርስ ነቀርሳ እናተርፋለን። ስሙንም ታሪክ እንለዋለን!
ዘውግ ለዘውግ፣ ጎሣ ለጎሣ፣ ነገድ ለነገድ፣ ሃይማኖት ለሃይማኖት፣ መንግስት ለመንግስት የጠብ ፈትል እናወርዳለን። ስለተቃጠለ ቤት መነጋገር አቅቶን ስለ አገር መቃጠል እናወጋለን። ዘመን ወደ ዘመን ሲሸጋገር ወገንና ወገን የሁለት ዓለም ሰዎች ሆነው ቁጭ ይላሉ።
የሁለት ዓለም ሰዎች ተረት፣ የሁለት ዓለም ሰዎች ታሪክ ነው ብለን The Tele of Two People የሚለውን፤ History of Two Worlds እያልን እንፅፋለን። የሁለት ሰዎች ተረት የሁለት ዓለም ሰዎች ታሪክ ይሆንና ያርፋል እንደማለት ነው። ሀገራችን የዚህ ዓይነት ታሪክ በየዘመኑ አይታለች። በታዋቂው የጥንቸልና የዔሊ ውድድር የልጅነት ታሪክ፤ ጥንቸል ዔሊን በመናቋ ተኛች። ዔሊ በቀርፋፋ ግን በማያቋርጥ ጉዞ ቀደመቻት። እንደ ዔሊም ተንቀርፍፈን ነገር ቢገባን እንዴት መታደል ነበር!
“አንዱ ቅጠል እሺ፣ አንዱ ቅጠል እምቢ” ይላሉ ፖርቹጋሎች ሲተርቱ። መደማመጥ መግባባትና መስማማት እየተቸገርን ስንት ዘመን ተጉዘናል። ይሄ ትንሣኤ በአል፤ ትንሳኤውን ይስጠን!!
ቻርለስ ዲከንስ በ“የሁለት ከተሞች ወግ” መጽሐፉ (The Tele of Two Cities) ሲጀምር “ከጊዜ ሁሉ ጥሩ ጊዜ ነው። ከጊዜ ሁሉ የከፋ ጊዜ ነው። የጠቢባን ዘመን ነው። የጅሎችም ዘመን ነው። የዕምነት ዘመን ነው። የክህደትም ዘመን ነው። የብርሃን ወቅት ነው። የጨለማ ወቅት ነው። የተስፋ ፀደይ ጊዜ ነው። ተስፋ - አስቆራጭ የክረምት ጊዜ ነው። ፊታችን ሁሉም ነገር አለ። ፊታችን ምንም ነገር የለም። ሁላችንም ወደሌላኛው ቦታ እየሄድን ነው” ይላል።
እንደኛ አብዮት ግራ የተጋባ የፈረንሳይ አብዮት ገጥሞች ነው። መልካም መልካሙን ለመሰብሰብ ቀና ልቦና ይስጠን!
በተለይ እንደኛ መልከ - ብዙ ህዝብ ባለበት አገር አንዱን መልክ ለይቶ ማየት አይቻልም። ሁሉም ታሪኬ የሚለው፣ ሁሉም እውነቴ የሚለው፤ የየራሱ አመጣጥ አለው። ችግሩ፤ የሚናገርበት ግላዊ መንገድ አለውና መግባባት ጠፋ!! አየርላንዳውያን “እያንዳንዱ ተረት የሚነገርበት ሁለት መንገድ አለው” የሚሉት ለዚህ ነው!
ለማናቸውም ታሪካዊ የህዝብ አዛዥ ታዛዥ መሆን፤ ሦስት መሰረታዊ ነገሮችን ዋቤ ያደርጋል። አንደኛ/ታዘዙ የሚባሉት ህዝቦች ድምፅ እንዳላቸው ሲሰማቸውና ቢናገሩ የሚደመጡ መሆናቸውን ማመን አለባቸው። ሁለተኛ/ ህጉ ተተንባይ (prediticable) ነገም የሚታይ የሚታወቅ መሆን አለበት። በቅጡ ለመገመት በሚቻል መልኩ የዛሬው ህግ ነገ ከሞላ ጎደል ያው ነው ተብሎ የሚታሰብ መሆን አለበት። ሦስተኛ/ባለሥልጣኑ ወይም ገዢው ክፍል ሁሉን እኩል፣ ሁሉን ያለ አድልዎ የሚያይ መሆን አለበት። እንግዲህ፤ የህዝብ ድምፅ፣ ተተንባይ ህግ እና ኢወገናዊነት ሦስቱ ቁልፎች ናቸው። የአባት ያያቶች ታሪክ ምን እንከን፣ ጉድለት ወይም መሰረታዊ አሊያም ተፈጥሮአዊ ህፀፅ እንዳለው መመርመርና በለሆሳስ ማጤን የሁሉም ወገን ግዴታ ነው። ብዙ፤ ሳናገኝ የቀረነው ነገር አለ። ከፖለቲካዊ ነፃነት እስከ እኮኖሚያዊ ነፃነት! የጀርባ አመጣጥና አካሄዳችን በቁጡና በለሆሳስ ካላስተዋልነው፤ የዛሬው ሁሉ - በጄ - ሁሉ በደጄ - ሊሆንልኝ አይችልም። የዝንጀሮ ልጅ እናቱን “ቅቤ ስጪኝ” ቢላት፤ “ቅቤ ቢኖር ያባትህ ታፋ ይህን ይመስል ነበር ወይ? አለችው”፣ የሚለው የጉራጊኛ ተረት፤ ልብ በሉ እሚለን ይሄንኑ ነው።
የትንሣኤንን በዓል በየአቅጣጫው ትንሳኤ አድርጎት ፍቅርና ሰላምን ያጎናፅፈን!!”   

Published in ርዕሰ አንቀፅ
Saturday, 19 April 2014 11:48

የፋሲካ ሰሞን ሶስት ወጎች

       የፋሲካ ሰሞን ነው። ልክ የዛሬ አንድ መቶ አርባ ስድስት ዓመት። በሚያዝያ ወር መጀመሪያ 1860 ዓ.ም። ሥፍራው በጎንደርና ወሎ መዋሰኛ ግድም እሚገኘው መቅደላ ተራራ።
ከአምሥት ዓመት በኋላ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ተመርቆ ሥራ በጀመረ በዓመት ተመንፈቁ ሁለት መቶኛ ዓመት የልደት በዓላቸውን የምናከብርላቸው ታላቁ ኢትዮጵያዊ ንጉሥ።
መላ ህይወታቸውን በጦርነት እና ሁሌም “ታጠቅ!” በማለት ያሣለፉት ዓፄ ቴዎድሮስ፤ በህይወት ዘመናቸው የመጨረሻውን ጦርነት ያደረጉት መቅደላ ተራራ ላይ ከአውሮጳ የመጡ የእንግሊዝ ወራሪዎችን ጦር በመግጠም ነው። በሠላሳ ሰባት ዓመታቸው ንጉሥ የሆኑት የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ቴዎድሮስ፤ ጋፋት ላይ በአውሮጳውያን ባለሙያዎች አስቀጥቅጠው ያሠሩትን ሲጳስቶቦል የተሰኘውን መድፍ በሃያ ሺህ ጎበዝ ወደ መቅደላ ተራራ በማስጎተት በጄኔራል ናፒየር የሚመራውን የእንግሊዝ ወራሪ ጦር ለመግጠም ተሰናድተዋል። ከአክሱም ሥርወ መንግሥት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ በደሞዝ የሚተዳደር የሰለጠነ ሰራዊት (Professional Army) ያቋቋሙት ቴዎድሮስ፤ በመጨረሻው ሰዓት ሁሉም ከድቶአቸው ከስልሳ ሺ የሰለጠኑ ወታደሮቻቸው መሃከል አራት ሺህ ብቻ ቀርተዋቸው ነበር። ከጦርነቱ በኋላ ሊረዳቸው የመጣውም ከአምስት ልጆቻቸው ከአልጣሸ ቴዎድሮስ ቀጥሎ ሁለተኛ ልጅ የሆነው ደጃዝማች መሸሻ ቴዎድሮስ ነው።
“የመቅደላ ጦርነት የተደረገው በፋሲካ ሰሞን ሚያዝያ አምስትና ስድስት ግድም ነው። ከነዚህ ቀናት ጥቂት ቀደም ብሎ ንጉሥ ቴዎድሮስ መቅደላ ደርሶ ጦር ለሚገጥማቸው ጄነራል ናፒየር አንድ ሺህ በጎች ላኩለት …” ሲል ፅፏል። ደፋሩና አመፀኛው ደራሢ አቤ ጉበኛ።  አቤ ጉበኛ “አንድ ለእናቱ” ያለው ቴዎድሮስን ነው፤ እርሡ አንድ ብቸኛው ኢትዮጵያዊ ኃያል ንጉሥ … ለማለት። “ከጦርነቱ ፍጻሜ በኋላ የቴዎድሮስ ሞት ለቴዎድሮስ እረፍት ለኢትዮጵያ ሀፍረት ነበር …. ሲልም ገልጿል ደራሲው።
“ክርስቲያን መሆንህን አውቃለሁ፤ ስለዚህ የሁዳዴን ፆም ፍታና (ፈሥክና) እኔን ግጠም …” ከሚል መልዕክት ጋር አንድ ሺህ በጎች የተሠደዱለት ጄነራል ናፒየር፤ መልእክቱንም በጎቹንም ተቀብሎ የሰሜን ኢትዮጵያንና የማዕከላዊ ሰሜን ኢትዮጵያን ከፍተኛና ተራራማ የመሬት ገፆች አቆራርጦ መቅደላ ደረሰና ከጀግናው ኢትዮጵያዊ ንጉሥ ቴዎድሮስ ጋር ጦር ገጠመ። ሲጳስቶቦል በቴዎድሮስ ትዕዛዝ ሁለት ጥይት ተኮሰና ሶስተኛው ላይ ፈነዳ። ሢጳስቶቦል ሲፈነዳ ቴዎድሮስ በቁጣ በነደደ መንፈሥ ተውጠው ጥርሣቸውን ሲያንቀራጭጩ፤ የጥርሣቸው መንቀራጨጭ በአካባቢው ላሉት ተዋጊዎች ይሠማ ነበር።  በመጨረሻ ቴዎድሮስ ኃይልና ቁጣ የተቀላቀለበት፣ ኢትዮጵያዊ ጀግንነት የተለኮሰበት ቃል ተናግረው፣ ሽጉጣቸውን ጠጡ። ራሳቸውን ሰው። መቅደላ አፋፉ ላይ ጩኸት በረከተ፤ የሴቱን አናውቅም ወንድ አንድ ሰው ሞተ፤ መቅደላ መቅደላ አንቺ ክፉ ጎራ ሴቱን ሁሉ ንቆ ሢኮራ ሲኮራ ወንዱ አንቺን ወደደ ተኛ ካንቺ ጋራ፤ ገደልን እንዳይሉ ሞተው አገኟቸው ማረክን እንዳይሉ ሰው የለ በጃቸው ምናሉ እንግሊዞች ሲገቡ አገራቸው?...
ጄነራል ናፒየር፡- የቴዎድሮስን የመጨረሻ ሚስት እቴጌ ጥሩወርቅን እና የመጨረሻ ልጃቸውን ህፃኑን ልጅ (ልዑል) ዓለማየሁን ይዞ ወደ አውሮጳ አቀና። እቴጌ ጥሩ ወርቅ አውሮጳ ከመድረሣቸው በፊት መንገድ ላይ አረፈች። ከማረፏ በፊት… ኃያል ጀግና ንጉሥ ባሏን “እጅህን ሥጥ!” … ባለች ጊዜ ከንጉሥ ቴዎድሮስ አንደበት የወጣው የቁጣ ቃል በአእምሮዋ ጓዳ እንደሚደውል ተሥፋ አደርጋለሁ። “እጅ የለኝም የሚሰጥ” ነው ያሉት ንጉሥ ቴዎድሮስ
እጄ እሣት ነው! ኃይለኞችን እንደ ህፃን በክንዱ ጨብጦ የኖረ እንደኔ ያለ ወታደር በጠላት እጅ መያዝን ሊታገሥ አይችልም! ልጅ ዓለማየሁ ለንደን ከደረሰ በኋላ የቤተ መንግሥት ኑሮ አልተመቸውም ነበርና በወቅቱ የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ወደነበረችው ህንድ ከአንድ እንግሊዛዊ የጦር መኮንን ጋር ሰደዱት። በዚያም ጤናው በመስተጓጎሉ በአሥራ ሰባት ዓመቱ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል። ለንደን ከተማ በሚገኘው የልጅ ዓለማየሁ መካነ መቃብር ላይ የአበባ ጉንጉን ያኖረ ኢትዮጵያዊ መሪ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር መለሥ ዜናዊ አሥረሥ (ክቡር መልከ ፀዲቅ) ነው። በመጨረሻ ጦር ቢገጥሙትም ከቴዎድሮስ የልብ ወዳጆች አብዛኞቹ እንግሊዛውያን ናቸው። በኢትዮጵያ ታሪክ የመጀመሪያው የቁንጅና ውድድር የጥምቀት ዕለት ወንዝ ዳር ተደርጎ አሸናፊዋን ቆንጆ ለእንግሊዛዊው ጆን ቤል የዳሩለት ንጉሥ ቴዎድሮስ ናቸው። ጆን ቤልን ኢትዮጵያዊ መጠሪያ አውጥተውና ኢትዮጵያዊ ሹመት ሰጥተው ሊቀ መኳሥ ዮሀንስ በማለት ኢትዮጵያዊ አደረጉት። በደብረ ታቦር ውጊያ ከመሞቱ በፊት ሊቀ መኳሥ ዮሀንስና ቴዎድሮስ በፈረሥ ሲሄዱ ልብሷ በላይዋ ላይ ያለቀ ሴት አገኙ። ቴዎድሮስ ከፈረሳቸው ወርደው ኪሣቸውን ቢዳብሱ አንዳች አጡ። ሊቀ መኳስን አበድረኝ አሉት። አምስት ማርትሬዛ ብር ሰጣቸው። ቴዎድሮሥ አምስቱን ማርትሬዛ ብር ለጎስቋላይቷ ሴት ሲሰጧት በጣሙን ተደሰተች። ሊቀ መኳስ ዮሀንስ በፃፈው ፅሁፍ ላይ እንዳወሳው፡- “ሥንመለሥ አምስት ማርትሬዛ ብር የነበረውን መቶ ማርትሬዛ ብር አድርገው ሰጡኝ” ብሎአል።
*   *   *
የፋሲካ ሰሞን፡- የትንሳኤ ሰሞን ማለት ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ በተሰቀለበትና ከሞት በተነሳበት ሰሞን።
ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት ኢየሱስ ክርስቶስ ከመስቀሉ ጥቂት ቀደም ብሎ ከእስር ቤት የተፈታ ሰው ነው በርባን። ህዝቡ በወቅቱ አይሁድን ሲገዛ ለነበረው ለሮማዊው ንጉሥ ጴላጦስ፣ “በርባን የተባለውን ወንበዴ ፍታልንና በምትኩ ኢየሱስን ሥቀለው!” በማለቱ ነው በርባን የተፈታው። በመፅሀፍ ቅዱስ ላይ በዝርዝር ያልተፃፈውን የበርባንን ሁለንታ “በርባን” በሚል ርዕስ መፅሀፍ የፃፈለት ደራሲ ከፍተኛውን ዓለም አቀፍ ሽልማት (Nobel Prize) ተሸልሟል። ይህንን መፅሀፍ ወደ አማርኛ የተረጎመው ኢትዮጵያዊው የፅሁፍ ጥበብ ሊቅ ዓቢይ ደምሤ ነው።
በርባን ከእሥር ቤት ከተፈታ በኋላ “ይሄ በእኔ ምትክ የተሰቀለው ሰው ማነው? እንዴት ያለ ሰው ነው?” ብሎ አርብ ዕለት ከሰዓት በሥቲያ በጎለጎታ ጌተሰማኒ ቀራንዮ መስቀል ላይ ኢየሱስ ክርስቶሥ በሁለት ወንበዴዎች መሃል ሆኖ ሲሰቀል ተደብቆ ተመልክቷል። ይህን ባየ ጊዜ መንፈሡ በጥልቅ ፍቅር ተመታ። ያ እናትና አባቱን የገደለ፣ ባገኘበት ቦታ ሴቶችን እያገላበጠ የሚዳራ፣ በውንብድና አገር ምድሩን የሚያምስ “ከፈሡ የተጣላ ሠው”፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሰቀል ባየ ጊዜ አእምሮው ተለወጠ። ስለዚህ በእርሱ ምትክ ስለተሰቀለው ሰው ሲጠይቅ “ከሶስት ቀን በኋላ ከሞት ይነሣል!” … ብለው ነገሩት። በአንዲት ሴት ወዳጁ ቤት ጭምት ሆኖ ጣሪያ ጣሪያውን እያየ እሁድ ሌሊት እስኪደርስ ተጠባበቀ። እሁድ ሌሊት ለቅዳሜ አጥቢያ ከሌሊቱ ዘጠኝ ሰዓት ግድም ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞት በተነሳበት ወቅት በርባን ተደብቆ መካነ መቃብሩ አጠገብ ተገኝቶ ነበር። መፅሀፍ ቅዱስ ላይ እንደምናየው ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞት መነሣቱን፣ መቃብሩ ባዶ መሆኑን ለመጀመሪያ ጊዜ ያየችው ማርያም መቅደላዊት ነች። እንዲሁም ደግሞ ሽቶ እጣን ይዘው የመካነ መቃብሩን ቅድሥና ሲንከባከቡ የነበሩ ጥቂት የሚወድዱት ሴቶች። ይሁንና በርባን በዚያ ነበር። የበርባን ህይወት ጨርሶ የተለወጠው ደግሞ ከዚህ በኋላ ነው።
በርባን በመጨረሻ ህይወቱ ያለፈው ሮም ውስጥ እነ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስና ሌሎች የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታዮች በእምነታቸው ሳቢያ በስቅላት ሲቀጡ፤ እርሱም በመሰቀሉ ነው።
በኢየሱስ ክርስቶስ ምክንያት ከእስራትና ከመሰቀል የዳነው (ድኖ የኖረው) ከብዙ ዓመታት በኋላ በኢየሱስ ክርስቶስ ምክንያት (ኢየሱስን በማመኑ) በስቅላት ተቀጣ። የጥንት ሮማውያን ጴጥሮሥን ዘቅዝቀው ሠቀሉት። ሌሎች የኢየሡሥ ክርስቶስን ተከታዮች ደግሞ መለመላቸውን በቁማቸው ሠቀሏቸው።
*   *   *
በ1888 ዓ.ም ከአንድ መቶ አስራ ስምንት ዓመታት በፊት የመቀሌ፣ የአምባላጌና የአድዋ ጦርነቶች የተደረጉት በሁዳዴ ፆም ውስጥ ነው። ጀግና የኢትዮጵያ ገበሬ ሰራዊት እህል ባፉ ሳይዞር እየፆመ ይዋጋል። በወቅቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ግብፃዊው አቡነ ማቲዎስ አቡኑ ከንጉሡና ከንግሥቲቱ ጋር ሆነው ወደ አድዋ ከሚተምመው የኢትዮጵያ ገበሬ ሰራዊት ጋር ናቸው። እስከ ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት ድረስ የጥንት የኢትዮጵያ ጳጳሳት ተቀብተው የሚመጡት ከግብፅ አገር አሌክሳንድርያ ከተማ ነበር።
አቡነ ማቲዎስ፤ “አሁን ጊዜው የጦርነት ስለሆነ ሰራዊቱን ይፍቱትና እየበላ እየጠጣ ይዋጋ .. ቢባሉ አሻፈረኝ አሉ። ቢባሉ ቢሰሩ በአሻፈረኝ ባይነታቸው የፀኑ ሆኑ። አልፈታም …አሉ። ስለዚህ የኢትዮጵያ የገበሬ ሰራዊት እየፆመ ለመዋጋት ተገደደ” የሚለን ደራሲና ጋዜጠኛ ጳውሎስ ኞኞ “አጤ ምኒልክ” በተሰኘ መፅሀፉ ላይ ነው።
ሰላምዎ ይብዛ! በፍቅር!
Soli-Deo-Gloria!
(ክብር ለእርሱ ይሁን!)

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 19 April 2014 11:44

የዓውዳመት ገበያ

   ሰፊ የበአል ሸመታ ከሚከናወንባቸው የአዲስ አበባ የገበያ ስፍራዎች የአቃቂ እና የሳሪስ ገበያዎች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ማክሰኞ እና ቅዳሜ በሚውለው የአቃቂ ገበያ እንዲሁም ረቡዕና ቅዳሜ በሚውለው የሳሪስ ገበያ የበግ ዋጋ ከአነስተኛ እስከ ትልቅ ከ900 እስከ 2200 ብር ሲጠራ፣ በሬ ከ7ሺህ እስከ 12ሺህ ብር፣ ዶሮ ከ85 እስከ 170 ብር፣ እንቁላል አንዱ 2፡50 ብር፣ ቅቤ 1ኛ ደረጃ 160ብር በኪሎ፣ 2ኛ ደረጃ 145ብር፣ ሽንኩርት 15.50 እና 16 ብር በኪሎ ሲሸጡ ሰንብቷል፡፡
በሸመታ ወቅት ስለ ግብይቱ ካነጋገርናቸው ሸማቾች አንዷ ወ/ሮ ቀለሟ ደጉ፤ ለበአል አስፈላጊ የሆኑትን ግብአቶች አስቀድመው መሸመታቸውን ገልፀው፣ የሽንኩርት ዋጋ በቀናት ልዩነት ከ7.50 ወደ 15.50 ብር ከፍ ከማለቱ ውጪ ካለፈው የገና በአል የተለየ የዋጋ ልዩነት በአብዛኞቹ ሸቀጣ ሸቀጦች ላይ አለማስተዋላቸውን ገልፀዋል፡፡ በሳሪስ ገበያ አግኝተን ያነጋገርናቸው ሌላዋ እማወራ የዘንድሮው በአል ገበያ የተረጋጋ መሆኑን ጠቅሰው የዳቦ ዱቄት ላይ ዋጋ ባይጨመርም በአብዛኞቹ ሱቆች የለም እንደሚባልና እጥረት መፈጠሩን ጠቁመዋል፡፡
በሳሪስ ገበያ የሸቀጣ ሸቀጥ ነጋዴ የሆነው ወጣት በበኩሉ፤ በዘንድሮው የፋሲካ በአል ላይ መንግስት ከውጭ የሚያስገባቸው ባለ 3 እና ባለ 5 ሊትር ዘይት እጥረት መፈጠሩንና አብዛኛው ሸማች በሊትር 42፡50 የሚሸጠውን የኑግ ዘይት ለመሸመት እንደተገደደ ገልጿል፡፡ ወደ ሱቁ ጐራ የሚሉ ደንበኞች ከውጭ የሚገባው ዘይት በቀላሉ እንደማይገኝ እንደሚጠቁሙት የተናገረው ነጋዴው፤ እጥረቱ የተፈጠረው ጅምላ አስመጪዎች ለቸርቻሪዎች በሚፈለገው መጠን እያቀረቡ ባለመሆኑ ነው ባይ ነው፡፡  
የበዓል ገበያ በሾላ
ወደ አዲሱ ገበያ መስመር ሲጓዙ በሚገኘው ሾላ ገበያ በዓሉን ሞቅ ደመቅ ለማድረግ ዶሮ፣ ሽንኩርት፣ ቅቤና በግ ለመግዛት አባወራዎችና እማወራዎች ከወዲህ ወዲያ ይላሉ፡፡ ወ/ሮ ሰላማዊት አበራ፤ ሽንኩርት 16 ብር መግባቱ ሻጩና ሸማቹ ያመጣው ትርምስ እንጂ የሽንኩርት እጥረት ተከስቶ እንዳልሆነ ይናገራሉ “ከዚህ በፊትም በእንቁጣጣሽ ጊዜ ሽንኩርት 20 ብር መግባቱን አስታውሳለሁ፡፡ ሸማቾችም በዓል ሲሆን እናበዛዋለን፡፡ ሻጩም የሸማችን ፊት እያየ ዋጋ ይቆልላል” ሲሉ አማረዋል፡፡ በመሆኑም ደረቅና ጥራት ያለው ሽንኩርት በ16 ብር ሲሸጥ መለስ ያለ ጥራት ያለው በ14 እና በ15 ብር እየተሸጠ ነው፡፡
ሀሙስ ዕለት ነው ያነጋገርነው የዶሮ ነጋዴው አቶ ለሚ፤ በዓሉ እየቀረበ ሲመጣ ቅዳሜ ዶሮ እየተወደደ እንደሚሄድ ይናገራል፡፡ በሾላ ገበያ ባለፉት ስምንት ዓመታት በተለያዩ በዓላት ዶሮ በመሸጥ ስራ ላይ መሰማራቱን የሚናገረው አቶ ለሚ፤ ነጋዴው የሸማቹን ፍላጎትና ሽሚያ እያየ ዋጋ እንደሚጨምር በመግለፅ፣ የወ/ሮ ሰላማዊትን ሀሳብ ይጋራል፡፡ “ረቡዕ እለት ጥሩ ስጋ አለው የሚባለውን ትልቅ ዶሮ በ190 ብር እንደሸጠ የሚናገረው አቶ ለሚ፤ ዛሬ (ሐሙስ) ከዚያው ዶሮ ጋር ተመጣጣኝ የሆኑ ዶሮዎችን በ240 ብር እየሸጠ እንደሆነ ገልጿል፡፡ ተዘዋውረን ለማየት እንደሞከርነው ዶሮ ከ110 ብር እስከ 235 ብር ድረስ እየተሸጠ ነበር፡፡
በሾላ ገበያ ለጋ ቅቤ በ180 ብር ሲሸጥ መካከለኛው 160 ብር በሳሉ ደግሞ 145 ብር በመሸጥ ላይ ይገኛል፡፡ ወ/ሮ ወርቅነሽ አባተ የተባሉ ቅቤ ነጋዴ፤ ከበዓል በፊትና በኋላ የቅቤ ዋጋ ብዙ ልዩነት እንደሌለው የገለፁ ሲሆን በበዓል ሰሞን በኪሎ ከአምስት ብር በላይ እንዳልጨመረ ተናግረዋል፡፡ ከነጋዴዋ ጋር ስለዋጋ በምንነጋገርበት ጊዜ ጣልቃ የገቡ አንድ እናት፤ በበዓሉ የቅቤ ዋጋ መጨመሩን ገልፀው ከአንድ ወር በፊት ጥሩ የሚባለው ቅቤ በ130 ብር ይሸጥ እንደነበር መስክረዋል፡፡
ከመቼውም በበለጠ በበዓል ሰሞን ገበያ የሚደምቀው ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጀርባ የሚገኘው ሾላ ገበያ ለዘንድሮው ፋሲካ በሰው ተጨናንቋል፡፡ እንቁላል በ2.50 እየተሸጠ ሲሆን የተዘጋጀ በርበሬ በኪሎ 85 ብር፣ በግ ከትንሽ እስከ ትልቅ ከ850 ብር እስከ 2800 ብር መሆኑን የገለፁልን በግ ነጋዴዎች፤ በዓሉ ቀረብ እያለ ሲመጣ የበግ ዋጋ ሊጨምር እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
ዘመናዊ ገበያዎች የበዓል አማራጮች ሆነዋል
ድሮ ዓመት በአል ሲመጣ አብዛኛው ሴት ወደ መርካቶ ነበር የሚሮጠው፡፡ አሁን ጊዜው ተለውጧል፡፡ በየአካባቢው በተከፈቱ ሱፐር ማርኬቶች የሚፈልጉትን ስለሚያገኙ መርካቶ መሄድ ትተዋል፡፡ መገናኛ ሸዋ ሃይፐር ማርኬት ዕቃ ስትገዛ ያገኘኋትን ሴት “ከመርካቶና ከዚህ ገበያው የቱ ይሻላል?” አልኳት “ያው ነው፤ እንዲያውም እዚህ ይሻላል፡፡ ምክንያቱም መርካቶ የምታገኘውን ሁሉ እዚህም ታገኛለህ፡፡ ጥራጥሬው፣ ቅመማ ቅመሙ፣ አትክልቱ፣ ፍራፍሬው፣ ዱቄቱ፣ ዶሮው፣ ሥጋው፣ አይቡ፣ የልጆች ልብስ ብትል፣ ጌጣጌጡ፣ … ኧረ ሁሉም ሞልቶአል፤ በዚህ ላይ መንገዱ ስለተቆፈረ መርካቶ መሄድ ስለማይፈልጉ ትራንስፖርት አስቸጋሪ ነው፡፡ ዋጋውስ? ያልክ እንደሆነ የትራንስፖርቱን፣ ያውራጅ ጫኚውን ስትደምርበት ያው ነው፡፡ በዚህ ላይ ፀሐይዋ! አናት ትበላለች ሳይሆን ልብን ነው የምታጥወለውለው፡፡ ኧረ ምን አገኝ ብዬ ነው የምንከራተተው?...” አለች፡፡
በሸዋ ሃይፐርማርኬት የሀበሻ ዶሮ 84 ብር፣ የፈረንጅ እንደኪሎው ከ136 ብር እስከ 178 ብር፣ በጣም ትልቁ ደግሞ 202 ብር፣ የክትፎ ሥጋ አንድ ኪሎ 126 ብር፣ የወጥ 110 ብር፣ የበግ ሥጋ አንድ ኪሎ 93 ብር፣ አንድ ኪሎ አይብ 60 ብር፣ ትልልቅ ቀይ ሽንኩርት 22 ብር፣ ነጭ ሽንኩርት 45 ብር ይሸጣል፡፡  
ገርጂ መብራት ኃይል አካባቢ ባለው ኦልማርት ያገኘኋትን ሴት፣ “ገበያው እንዴት ነው? ከዚህና ከውጪው የቱ ይሻላል?” አልኳት፡፡ “ያው ነው፤ ብዙ ልዩነት የለውም፡፡ አንዳንድ ዕቃ ጥራቱን ስታይ እዚህ ይሻላል፤ ውጭ ደግ ጥራቱ ቀነስ ያለ በቅናሽ ዋጋ ታገኛለህ” እስቲ ለምሳሌ ምን? አልኳት “ለምሳሌ ቀይ ሽንኩርት ብንወስድ እዚህ 21 ብር ከምናምን ነው፡፡ ትልልቅ ነው ጥራቱም ጥሩ ነው፡፡ ውጭ ከሆነ ከ15 እስከ 16 ብር ታገኛለህ፡፡ ነገር ግን መካከለኛ ወይም አነስ ያለ ነው፡፡…”
ለፋሲካ ዶሮ ገዝታ እንደሆነ ጠየኳት፡፡ እንዳልገዛች ነገረችኝ፡፡ ከየት ለመግዛት እንዳሰበች ስጠይቃት፣ ከሱፐር ማርኬት እንደምትገዛ ነገረችኝ፡፡ ለምን? አልኳት፡፡ “እኔ የኮንዶሚኒየም ነዋሪ ነኝ፡፡ እዚያ ዶሮ ለማረድና ለመገነጣል አይመችም፡፡ ቆሻሻ መድፊያው ያስቸግራል፡፡ ከላይ ታች መመላለሱም ይሰለቻል፡፡ ዋጋውም ያው ነው፤ የታረደውን ከዚሁ እገዛለሁ” በማለት ምርጫዋን ነገረችኝ፡፡
በኦል ማርት ሱፐር ማርኬት የፈረንጅ ዶሮ በኪሎ 133 ብር፣ የሀበሻ ዶሮ የተበለተ ከ133 እስከ 139 ብር፣ ቀይ ሽንኩርት 21.70፣ አንድ ኪሎ የበግ ስጋ 100 ብር፣ የበሬ 138 ብር፣ የጥጃ 110 ብር፣ የጭቅና ሥጋ 210 ብር፣ ቅቤ የተነጠረ 165 ብር (1 ኪሎ ግን አይሞላም)፣ ዕንቁላል 2.65 ይሸጣል፡፡ እዚያው አካባቢ የጎንደር የተጣራ የኑግ ዘይት አንድ ሊትር 44 ብር፤ አምስት ሊትር 235 ብር፡፡
ገርጂ ሰንሻይን ኮንዶሚኒየም ፍሬሽ ኮርነር በተባለ ሱፐርማርኬት የፈረንጅ ዶሮ በኪሎ 115 ብር፣ የተገነጣጠለ ሙሉውን የሀበሻ ደሮ 125 ብር፣ ያልተገነጣጠለ 100 ብር፣ አንድ ዕንቁላል 3 ብር፣ 10 ዕንቁላል 35 ብር፣ አይብ አንድ ኪሎ 60 ብር፣ ሽንኩርት በኪሎ 16 ብር፣ ነጭ ሽንኩርት 48 ብር፣ የተነጠረ ኪሎ ቅቤ 200 ብር፣ ሎሚ በኪሎ 35 ብር፣ ግማሽ ኪሎ 17 ብር፣ ለወጥ የሚሆን ሥጋ 100 ብር፣ የጥብስ 140 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

Published in ዜና

        ጋምቢያ የሚገኘው የአፍሪካ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በሽብር ተከሰው በእስር ላይ የሚገኙ “የሙስሊሙ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ” አባላት ያቀረቡትን የክስ አቤቱታ እንደተቀበለ ምንጮች ገለፁ፡፡
የኮሚቴው አባላት የክስ አቤቱታውን ያቀረቡት ከወራት በፊት ሲሆን በእነ አቡበከር አህመድ መዝገብ በሽብር የተከሰሱት 28 ግለሰቦች፤ ሙስሊሙ ማህበረሰብ ከአወሊያ ት/ቤት እና ሌሎች ሃይማኖታዊ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ ለተፈጠረው አለመግባባት በመፍትሔ አፈላላጊነት የመረጣቸው መሆኑን ጠቅሰው፤ መንግስት በሃይማኖት ጣልቃ መግባቱን በመቃወማቸው “አሸባሪ” ተብለው ለእስር መዳረጋቸውን ለኮሚሽኑ አመልክተዋል፡፡
“አህባሽ” የተሰኘውን የሊባኖስ አስተምህሮ በግድ በሙስሊሙ ህብረተሰብ ላይ ለመጫን የተለያዩ ስልጠናዎች መሠጠታቸውን የጠቆመው የክስ አቤቱታው፤ ይህን “የመንግስት አካሄድ” የታሠሩትን ጨምሮ ሙስሊም ኢትዮጵያውያን በሠላማዊ መንገድ ቢቃወሙም መንግስት የተቃወሙትን በማሰር፣ የሃይማኖት መሪዎችን ከሃላፊነታቸው በማንሣት፣ እስላማዊ ት/ቤቱን በመዝጋት መንግስት አፀፋዊ እርምጃ እንደወሰደ ያስረዳል፡፡
በጥር 2004 ዓ.ም “የሙስሊሙ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ” አባላት በችግሩ ዙሪያ ከተለያዩ የመንግስት አካላት ጋር ለመነጋገር መንግስት ከተስማማ በኋላ ቃሉን በማጠፍ፣ የኮሚቴውን አባላት እና ተቃውሞ ያሰሙትን አስሮ በአሸባሪነት ክስ እንደመሠረተባቸውም የክስ ማመልከቻው ያብራራል፡፡
በማረሚያ ቤት ሆነው የፍርድ ሂደታቸውን እየተከታተሉ መሆናቸውን የገለፁት ተከሳሾቹ፤  ከቤተሰቦቻቸው፣ ከህግ አማካሪዎቻቸው እና ከህክምና ባለሙያዎች ጋር እንዳይገናኙ መደረጉን፣ ቤተሰቦቻቸውም በፖሊስ ወከባ እንደደረሰባቸው በክስ ማመልከቻቸው ጠቁመዋል፡፡
ተቀማጭነቱን ጋምቢያ ያደረገው የአፍሪካ ሰብአዊና ህዝባዊ መብቶች ኮሚሽን የቀረበለትን የክስ አቤቱታ መርምሮ የሚያስተላልፈው ውሣኔ የሚጠበቅ ሲሆን የፍርድ ሂደቱን እስከማቋረጥ ሊደርስ የሚችል ውሣኔ ያሳልፋል ተብሎ እንደሚገመት ምንጮዎች ጠቁመዋል፡፡
በ1987 ዓ.ም በአፍሪካ ህብረት ስር የተቋቋመው ኮሚሽኑ፤ የህብረቱ አባል አገራት የህዝባቸውን ሰብአዊ መብት ማስጠበቅ አለማስጠበቃቸውን የመመርመር ስልጣን ያለው ፍ/ቤት እንደሆነ ያመለከቱት ምንጮች፤ ከሌሎች መሰል የሰብአዊ መብት ተቋማት በተሻለ ውሳኔው በአባል ሀገራቱ ተቀባይነት እንዳለው ገልፀዋል፡፡
በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት፣ የተከሣሾቹን ቃል የመስማት ሂደት ባለፈው አርብ ሚያዚያ 3 የተጠናቀቀ ሲሆን የመከላከያ ምስክሮችን ለመስማት ለግንቦት 4 ተቀጥሯል፡፡

Published in ዜና
Page 6 of 13