“በልማት ሰበብ አፈና የሚፈፀምበት መዋቅር ነው” - መኢአድ
“1ለ5 አደረጃጀት ለምርጫው ስጋት አይሆንም”  - አንድነት
“ፓርቲያችን፤ ህዝቡ የመዋቅሩ ሰለባ እንዳይሆን የማጋለጥ ሥራ ያከናውናል”  - መድረክ
“ተቃዋሚዎችም እንደ ኢህአዴግ የፈለጉትን አደረጃጀት መፍጠር ይችላሉ”  - መኢአብ
“ኢህአዴግ አፋኝ ሚሊሻ አድርጎ ያዘጋጃቸው ናቸው” - ኢዴፓ
“አደረጃጀቱን ለምርጫ ይጠቀማል የተባለው የሃሰት ውንጀላ ነው”  - ኢህአዴግ

መንግስት 1 ለ 5 የተሰኘውን አደረጃጀት ለፈጣን ልማታዊ እድገት እየተጠቀመበት እንደሆነ ይናገራል፡፡ በገጠር ይሄንኑ አደረጃጀት ለጤና ኤክስቴንሽን ሠራተኞች ተጠቅሞበት ባስገኘው ውጤት፣ ከኢትዮጵያ አልፎ ለአፍሪካ አገራት ምሳሌ ለመሆን መብቃቱንም በኩራት ይጠቅሳል፡፡ ተቃዋሚዎች በበኩላቸው፤ አደረጃጀቱ ፖለቲካዊ ግብን ያነገበ የስለላ መዋቅር ነው፣ የገዥው ፓርቲ የምርጫ ማስፈፀሚያና መቆጣጠሪያ መዋቅር ነው ሲሉ ይተቻሉ፡፡
ኢህአዴግ በ1 ለ 5  አደረጃጀት በመላው ሃገሪቱ የልማት እንቅስቃሴዎችን በማፋጠን ረገድ ስኬታማ እየሆንኩ ነው ቢልም ተቃዋሚዎች ግን ለአፈና እየተጠቀመበት ነው ይላሉ፡፡ “ከክልል ክልል፣ ከወረዳ ወረዳ ተዘዋውረን ህዝብን በአላማችን ስር ማሰለፍና ማደራጀት ቸግሮናል፣ አባላቶቻችንና ደጋፊዎቻችን እስራትና ድብደባን ጨምሮ ለብዙ እንግልት እየተዳረጉ ነው፣ እንኳንስ ሰፊ ህዝባዊ መሰረት ያለው አደረጃጀት ልንፈጥር በአንድ ወረዳ ውስጥ እንኳን  ፅ/ቤት መክፈት አቅቶናል፣ ከአዲስ አበባ ህዝብ የማደራጀት ተልዕኮ ተሰጥቷቸው የተሸኙ አመራሮች፣ የወረዳ ሹማምንት ሰለባ ይሆናሉ” የሚሉት ተቃዋሚ ፓርቲዎች፤ ገበሬው 1 ለ 5 ካልተጠረነፈ፣ ማዳበሪያና ምርጥ ዘር የመሳሰሉ የግብርና ግብአቶችን ማግኘት አይችልም ሲሉ ችግሮችን ይዘረዝራሉ፡፡
ኢህአዴግ 1ለ5 አደረጃጀትን ከምንም በላይ ለምርጫ ማስፈፀሚያነት ነው የሚፈልገው ሲሉ የሚከራከሩት ተቃዋሚዎች፤ በምሳሌነትም ያለፉትን ሁለት ምርጫዎች ይጠቅሳሉ፡፡ በ2002 ዓ.ም አገራዊ ምርጫ “ሊግ” እና “ፎረም” ኢህአዴግን በማስመረጥ ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል የሚሉት ተቃዋሚዎች፤ በ2005 ዓ.ም የአካባቢና ማሟያ ምርጫ ደግሞ የመንግስት ሰራተኛ የሆኑ የጤና ኤክስቴንሽንና የግብርና ባለሙያዎችን ጨምሮ በ1 ለ 5 አደረጃጀት በሚገባ ተጠቅሞባቸዋል ይላሉ፡፡ 12 ወራት ብቻ ለቀሩት ቀጣዩ ብሄራዊ ምርጫም ገዥው ፓርቲ እነዚህን የመንግስት መዋቅሮችና የህዝብ አደረጃጀቶች እንዲሁም ሌሎች አዳዲስ የአደረጃጀት ስልቶችን ለምርጫ ቅስቀሳ እና ድጋፍ ማሰባሰቢያ መጠቀሙ ፈጽሞ አያጠራጥርም፤ ምክንያቱም ከዚህ በፊትም አድርጐታል በማለት ሽንጣቸውን ገትረው ይከራከራሉ - ተቃዋሚዎች፡፡
“የገዥው ፓርቲ የጨዋታ ህግ 1 ለ 5፣ 1 ለ 40 እና 1 ለ 100 መሆኑን ደርሰንበታል” ያሉት የመላ ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ሊቀመንበር አቶ አበባው መሃሪ፤ “በልማት ሰበብ አፈና የሚፈፀምበት መዋቅር ነው” በማለት 1ለ5 አደረጃጀትን ይከሳሉ፡፡ ኢህአዴግ እንደሚለው ለልማት ብቻ ቢሆን ኖሮ፤ ተማሪዎች በ1 ለ5 ባልተደራጁ ነበር የሚሉት ሊቀመንበሩ፤ መዋቅሩ ገበሬውንና ነዋሪውን እንዲሁም የመንግስት ሰራተኛውን ከገዥው ፓርቲ አስተሳሰብ ውጪ እንዳይንቀሳቀሱ የሚያስር እንደሆነ ጠቅሰው፤ በመዋቅር ወደታች ከሚወርደው አስተሳሰብ ያፈነገጠም ቅጣት ይጣልበታል ብለዋል፡፡ “በገጠር የ1 ለ 5 አደረጃጀት አባል ያልሆነ ገበሬ፤  ማዳበሪያና የግብርና ግብአቶች እንዳያገኝ ከመከልከሉም ባሻገር ከሌላው የህብረተሰብ ክፍልም እንዲገለል ይደረጋል፡፡ መንግስት ይህን በማድረጉ አፈናውን አጠናክሮ መቀጠል ይችል ይሆናል፤ የህዝብ ተወዳጅነትንና ቅቡልነት ማግኘት ግን አይችልም፡፡” እንዲህ ዓይነቱ ሴራ ኢህአዴግን በ2007 ምርጫ ከመሸነፍ አይታደገውም የሚሉት አቶ አበባው፤ ይሁን እንጂ አደረጃጀቱ በመራጩ ህዝብ ላይ በነፃነት የፈለገውን እንዳይመርጥ ስጋት ማሳደሩ አይቀርም ባይ ናቸው፡፡ ምንም እንኳን ኢህአዴግ በአፉ ግልጽና ፍትሃዊ ምርጫ እንደሚካሄድ በተለያዩ አጋጣሚዎች ሲናገር ቢደመጥም፤ ይሄ አደረጃጀት ግን ትክክለኛ ምርጫ እንዳይካሄድ የአፈና መዋቅር መዘርጋቱን የሚያረጋግጥ ነው ብለዋል፤ አቶ አበባው፡፡ ይህን አስጊ መዋቅር ለመበጣጠስና ለማክሸፍ መፍትሄው በምርጫው ተሳታፊ የሆኑ ፓርቲዎች ሁሉ ህብረት ፈጥረው በጋራ መቆማቸው ነው ያሉት አቶ አበባው፤ መኢአድ የጉዳዩን አሳሳቢነት ከግምት ውስጥ በማስገባት ለሰብአዊ መብት ኮሚሽን፣ ለፍትህ ሚኒስቴር እና ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት የአቤቱታ ደብዳቤ ማቅረቡን ገልፀዋል፡፡
የአንድነት ፓርቲ የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ አቶ ዳንኤል ተፈራ በበኩላቸው፤ ፓርቲያቸው እስካሁን ህዝብን ለማደራጀት ባደረጋቸው እንቅስቃሴዎች በርካታ የአፈና ተግባራት እንደተፈፀሙበት ጠቅሰው፤ የ1 ለ 5 አደረጃጀት በምርጫው ላይ የሚፈጥረው ስጋት እምብዛም ነው ሲሉ ያቃልሉታል - መንግስትን መቀየር የፈለገ ህዝብ፣ የአፈና መዋቅር ሊገድበው እንደማይችል በመግለፅ፡፡ በአሁን ወቅት ፓርቲያቸው ከ34 በላይ በሚሆኑ የሀገሪቱ ዞኖች ቢሮዎችን በማደራጀት፣ ወደ ወረዳዎች ወርዶ  ለህዝቡ ተደራሽ ለመሆን እየጣረ መሆኑን የጠቆሙት ኃላፊው፤ በነዚህ ሂደቶች ውስጥ የወረዳ ሹማምንት የሚፈፅሙት ወከባና እንግልት ከአቅም በላይ እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡ በአዲስ አበባ አዳዲስ አባላት ፎርም ሞልተው ከፓርቲው ጽ/ቤት ሲወጡ ፀጉረ ልውጥ ግለሰቦች ክትትል ያደርጉባቸዋል የሚሉት አቶ ዳንኤል፤ ይሄም የአፈና መዋቅሩ ይበልጥ መጠናከሩን ይጠቁማል ባይ ናቸው፡፡  እንዲያም ሆኖ ግን ይህ ለፓርቲያችን ፈታኝ ጉዳይ ተብሎ ሊጠቀስ አይችልም ያሉት ኃላፊው፤ ህዝቡ ጋ ቁርጠኝነት መኖሩን በተለያዩ አጋጣሚዎች ስለተረዳን፣ ገዥው ፓርቲ 1 ለ 5ን ጨምሮ የተለያዩ መዋቅሮችን ዘርግቶ ዲሞክራሲያዊ እንቅስቃሴዎችን ለመገደብ እየሞከረ ቢሆንም፣ በምርጫው ለማሸነፍ የሚደረገውን ትግል አጠናክረን ከመቀጠል ወደ ኋላ አንልም ብለዋል፡፡
ኢህአዴግ ኃላፊነት የሚሰማውና ለመድብለ ፓርቲ መጐልበት የሚጨነቅ ፓርቲ አይደለም ሲሉ የተቹት አቶ ዳንኤል፤ ሁሌም ምርጫን ህገወጥ በሆኑ አደረጃጀቶች ለማሸነፍ ሲታትር ነው የሚታየው ብለዋል፡፡ የ1 ለ 5 አደረጃጀት፤ በዲሞክራሲ ግንባታ ሂደት ላይ ነኝ ከሚል መንግስት የማይጠበቅ ኢ-ዲሞክራሲያዊ የሆነ አደረጃጀት ነው ያሉት ሃላፊው፤ ይሄም ሳያንሰው በገጠሩ የሃገሪቱ ክፍል ሴፍቲኔት፣ ጤና ኤክስቴንሽንና የግብርና ኤክስቴንሽን የመሳሰሉ የመንግስት መዋቅሮችን ፓርቲው ለግል ጥቅሙ ያውላል ሲሉ ይከሳሉ፡፡ አሁን ደግሞ “የህዝብ ክንፍ” በሚባል አደረጃጀት እድሮችን፣ እቁቦችንና የመሳሰሉ ማህበራዊ ተቋማትን ለመቆጣጠር እየተሞከረ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ዳንኤል፤ ፓርቲያቸው እነዚህን መዋቅሮችና አደረጃጀቶች ለመስበር የተለያዩ ስልቶችን ነድፎ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የፓርቲው አባላት በአደረጃጀቱ ውስጥ ሰርገው እንዲገቡ በማድረግ መንግስት ለልማት በሚል የዘረጋውን መዋቅር፣ ለፖለቲካ አላማ እንዳያውል ቁጥጥር መጀመራቸውን ጠቁመዋል፡፡ በዚህም ተልዕኦ አባላቶቻቸው ውጤታማ የሆነ ተግባር እያከናወኑ እንደሆነ አቶ ዳንኤል አክለው ገልፀዋል፡፡
ምርጫ የገዥም የተቃዋሚ ፓርቲም አይደለም፤ ህዝብ የራሱን ውሳኔና አቅሙን የሚያሳይበት ነው የሚሉት የአንድነት ሃላፊ፤ “በሃገሪቱ ካለው ከፍተኛ የሆነ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ቀውስ አንፃር ገዥው ፓርቲ ያደራጀውን መዋቅር ፈርቶ ህዝቡ የምርጫ ካርዱን የማይገባ ቦታ አይጥልም” ሲሉ ይሟገታሉ፡፡ አቶ ዳንኤል ሃሳባቸውን ሲያጠቃልሉም፤ ፓርቲያቸው በተለያዩ የንቅናቄ መንገዶች ህብረተሰቡን ለማንቃት እየተጋ በመሆኑ፣ የ1 ለ 5 አደረጃጀት ለምርጫው ስጋት አይሆንም ብለዋል፡፡
“ገዥው ፓርቲ በተጨባጭ በ2002 ምርጫ  የ1 ለ 5 አደረጃጀትን ‘የምርጫ ሰራዊት’ ብሎ ለምርጫ አላማ እንደተጠቀመበት እናውቃለን” የሚሉት ደግሞ የመድረክ ሥራ አስፈፃሚ አባል አቶ ጥላሁን እንደሻው ናቸው፡፡ መድረክ እነዚህ አደረጃጀቶች በምርጫ ሂደት ውስጥ እንዳይገቡ በሚል እንደመደራደሪያ ያቀረበው ጥያቄ እስከዛሬ መልስ አለማግኘቱን የጠቆሙት አቶ ጥላሁን፤  በቀጣዩ ምርጫም የ1 ለ 5 አደረጃጀት ተፅዕኖ ላለማድረጉ ምንም ዋስትና የለም ሲሉ ስጋታቸውን ገልፀዋል፡፡ “በአደረጃጀቱ ውስጥ ጠርናፊ የሆነው ግለሰብ፣ ዋና ተግባሩ ሌሎች በስሩ ያሉ ግለሰቦችን እንቅስቃሴ መከታተል ነው” ያሉት አቶ ጥላሁን፤ ድርጊቱ የግለሰቦችን ነፃነት የሚፃረርና ኢ-ዲሞክራሲያዊ ነው ሲሉ ይነቅፋሉ፡፡
መዋቅሩ በዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ የሚያሳርፍ እንደሆነ የተናገሩት የመድረክ ሥራ አስፈፃሚ አባል፤ ፓርቲያቸው አሰራሩን በጥብቅ እየተቃወመ፣ ህብረተሰቡ የመዋቅሩ ሰለባ እንዳይሆን በተለያዩ መንገዶች የማጋለጥ ስራ ያከናውናል ብለዋል፡፡
አረና ትግራይ ለሉአላዊነት ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ጎይቶም ፀጋዬ በበኩላቸው፤ የ1 ለ 5 አደረጃጀት ለምርጫው እንቅፋት ሊሆን ይችላል የሚል ስጋት አላቸው፡፡ “ፍትሐዊና ሚዛናዊ ምርጫ ይካሄዳል የሚባል ከሆነ፣ የምርጫ ቦርድም ሆነ ገዥው ፓርቲ በዚህ ጉዳይ ላይ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር ድርድር ሊያደርጉ ይገባል” ባይ ናቸው፡፡ ኢህአዴግ አውራ ፓርቲ ሆኖ ለመቀጠል እነዚህን መዋቅሮች እየተጠቀመ ነው የሚሉት አቶ ጎይቶም፤ በልማት ስም የተዋቀረውን አደረጃጀት ለፖለቲካ አላማ ሊጠቀምበት እንደሚችል ጠቅሰው፤ አደረጃጀቱ በህዝቡ ዘንድ ተቀባይነት  እንዳይኖረው ማስገንዘብ ከፓርቲዎች ይጠበቃል ይላሉ፡፡
ኢህአዴግን ጨምሮ የተወሰኑ ተቃዋሚዎች የተካተቱበት የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አባል የሆነው የመላው ኢትዮጵያውያን ብሄራዊ ንቅናቄ (መኢአብ) ሊቀመንበር አቶ መሳፍንት ሽፈራው ግን የሌሎቹን ተቃዋሚ ፓርቲዎች ሃሳብና ስጋት አይጋሩም፡፡ እንደውም ተቃዋሚዎቹን ይወቅሳሉ፡፡ የማደራጀት መብት ለኢህዴግ ብቻ አልተሰጠም ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ይህን መብት የመጠቀም የቤት ስራቸውን በአግባቡ ስላልተወጡ ነው የተበለጡት ይላሉ፡፡ ተቃዋሚዎችም እንደ ኢህአዴግ የፈለጉትን አደረጃጀት መፍጠር ይችላሉ የሚሉት አቶ መሳፍንት፤ የ1 ለ 5 አደረጃጀት ችግር ሊፈጥር የሚችለው ለልማት ተብሎ የተቀየሰው መዋቅር ለፖለቲካ አላማ ከዋለ ነው ሲሉ ወደ ተቃዋሚዎች ሃሳብ ይመለሳሉ፡፡ ፓርቲያቸው ጉዳዩን ለመገምገም እየተዘጋጀ መሆኑን በመጠቆምም ከግምገማው በኋላ መግለጫ እንደሚሰጡበት ተናግረዋል - ሊቀመንበሩ፡፡
የኢትዮጵያውያን ዲሞክራቲክ ፓርቲ (ኢዴፓ) ሊቀመንር አቶ ጫኔ ከበደ በበኩላቸው፤ ጉዳዩን ቁጭ ብለው እንደገመገሙት  ይናገራሉ፡፡ “መንግስት የልማት ቡድን ነው ይላል፤ ኢህአዴግ እንደ ፓርቲ ደግሞ ዴሞክራሲያዊ ስርአት በዚህች ሃገር እንዳይሰፍን የአፈና ሚሊሻ አድርጎ ያዘጋጃቸው ናቸው በሚል ነው በግምገማችን የፈረጅናቸው” ያሉት ሊቀመንበሩ፤ መዋቅሩ በቀጣይ ምርጫ ችግር ፈጣሪ እንቅፋት ይሆናል የሚል ስጋት አለን ይላሉ፡፡ የማደራጀት መብት የተቃዋሚ ፓርቲዎችም ነው የሚለው አባባል አያስማማንም የሚሉት አቶ ጫኔ፤ እንኳንስ በህዝቡ ውስጥ ዘልቆ አጀንዳን ለማስረፅ ይቅርና ሦስትና አራት ሆኖ የተሰበሰበም በጥርጣሬ የሚታይበት ሃገር ላይ ነው ያለነው ሲሉ ችግሩን ያስረዳሉ፡፡ ኢዴፓ አፈናውን ለመቋቋም ሚስጥራዊ አደረጃጀቶችን ይጠቀማል ያሉት ሊቀመንበሩ፤ መዋቅሩን ፓርቲያቸው እንደማይቀበለውና ድርጊቱንም “አፋኝ ሚሊሻዎችን እንደማደራጀት” እንደሚቆጥረው ተናግረዋል፡፡
ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ አንድ የፖለቲካ ምሁር እንደሚሉት፤ ገና ከአሁኑ የተነሳው ውዝግብ በምርጫ ማግስት ለሚከሰቱ ቅራኔዎችና አለመግባባቶች ትልቅ ሰበብ ሊሆን ስለሚችል፣ ኢህአዴግን ጨምሮ ፓርቲዎቹ ሁሉ በጉዳዩ ላይ በሰለጠነ መንገድ ተወያይተው መግባባት ላይ መድረስ አለባቸው፡፡
በአንድ ክልል ከተማ ስለ 1ለ5 አደረጃጀት ግንዛቤ ለማስጨበጥ የተበተነ ሠነድ፣ አደረጃጀቱ በኢኮኖሚ ከበለፀገችው የጃፓን መንግስት የሚጠቀመው እንደሆነና ከዚያም እንደተኮረጀ ይጠቁማል፡፡ አላማውም የልማት ሠራዊት በመገንባት ዜጐችን በየተሠማሩበት ዘርፍ ብቁና ውጤታማ ለማድረግ እንደሆነ  ሰነዱ ያብራራል፡፡
በትምህርት ሚኒስቴር ተዘጋጅቶ የቀረበ ስለ አደረጃጀቶች የሚተነትን ሌላ ሰነድ ደግሞ ተማሪዎችን 1ለ5 ማደራጀት፣ ተማሪዎች በየትምህርታቸው ውጤታማ ሆነው እንዲጨርሱና የትምህርት ብክነትን ለመቀነስ ዋነኛ መፍትሔ መሆኑን ይገልፃል፡፡ የየቡድኑ ሃላፊነት እና ተግባርም የክፍሉ ተማሪዎች ውጤትና ስነምግባር ተቀራራቢ ደረጃ እንዲደርስ፣ የተሻሉ ተማሪዎች ሌሎችን እንዲረዱ፣ የተማሪዎች የመተጋገዝና የመረዳዳት ባህል እንዲዳብር፣ ያለአግባብ የትምህርት ክፍለጊዜ እንዳይባክን ማድረግና ሌሎችንም ይዘረዝራል፡፡
ያነጋገርናቸው የ1ለ5 አደረጃጀት ተሣታፊዎች በበኩላቸው፤ የስለላ አይነት መዋቅር ነው በማለት የተቃዋሚ  ፓርቲ መሪዎችን ሃሳብ ይጋራሉ፡፡ ስማቸው እንዳይገለፅ የጠየቁ የአንድ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ሠራተኛ እንደሚሉት፤ የአደረጃጀቱ አላማ በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ውስጥ ያሉ የሥራ ክፍሎች፣ በየዘርፋቸው ውጤታማ እንዲሆኑ  ምክክርና ውይይቶች የሚካሄድበት ቢሆንም የውይይቱ ፍሬ ሃሳብ ለበላይ አደረጃጀቶች ሪፖርት ሲደረግ፣ ተቃራኒ ሃሳብ ያንፀባረቁትን ግለሰቦች ለፖለቲካዊ ጥቃት ይዳርጋል፡፡ በመስሪያ ቤታቸው ውስጥ ያሉት አደረጃጀቶች በሙሉ በኢህአዴግ አባልነታቸው በሚታሙ ግለሰቦች እንደሚመሩ የገለፁት እኚሁ አስተያየት ሰጪ፤ ብዙውን ጊዜ በውይይትና በምክክር ወቅት ስለአብዮታዊ ዲሞክራሲና ስለልማት ትልሞቹ ገቢራዊነት በስፋት ይደመጣል ይላሉ፡፡ ይህም አደረጃጀቱ ከፖለቲካ ነፃ አለመሆኑን ያሳያል ባይ ናቸው አስተያየት ሠጪው፡፡ በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ከሚከተለው ርዕዮተ አለም ውጪም ሌላ ሃሳብ ማራመድ እንደማይቻል አክለው ገልፀዋል፡፡
በዚሁ መስሪያ ቤት ውስጥ ያለው የ1 ለ5 አደረጃጀት ተዋረዳዊ ሲሆን ከስር ያለው የ1 ለ 5 አደረጃጀት መሪ ከሌሎች አደረጃጀቶች መሪዎች ጋር እንደገና 1ለ5 ይደራጃል፤ እንደዚያ እያለ እስከ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ይደርሳል፡፡ ከላይ የሚቀመጠው ደግሞ የመንግስት ሹመኛ የሆነ ግለሰብ ነው ብሏል፡፡
በጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት የህዝብ ተሣትፎና አደረጃጀት ሚኒስትር ዲኤታ አቶ ደስታ ተስፋው፤ መንግስት ስለዘረጋው 1 ለ5 አደረጃጀት ሲያብራሩ፤ “አደረጃጀቱን በርካታ የእስያ ሃገሮችን ጨምሮ በአፍሪካ ውስጥም ታንዛንያን የመሳሰሉ ሀገሮች እየተጠቀሙበት ውጤታማ እየሆኑ ነው፤አደረጃጀቱ ህዝብን ለልማትና ለመልካም አስተዳደር አደራጅቶ ተግባራዊ ለማድረግ የተፈጠረ ነው፡፡ የህዝብን ጉልበት አስተባብሮ፣ በጋራ ተደራጅቶ ያሉበትን የአፈፃፀም ችግሮች በጋራ ቀርፎ እቅድ ላይም ተወያይቶ በጋራ የሚሠራበት አደረጃጀት ነው” ይላሉ፡፡ በዚህ ሂደትም ግቦቹ ሲሳኩ ተጠቃሚ የሚሆነው ራሱ ህብረተሰቡ ነው ይላሉ፤ አቶ ደስታው፡፡
ከላይ ጀምሮ እስከታች ያለው አደረጃጀት ዋና አላማው፣ በልማት ሠራዊት ተደራጅቶ እንዲንቀሳቀስ ማድረግ ነው የሚሉት ሃላፊው፤ የልማት ሠራዊት ሲባልም የተመጣጠነ ክህሎትና አስተሳሰብ በመፍጠር፣ ለልማትና ለመልካም አስተዳደር ማዋል ነው፣ በዚህ መንገድም የልማት ሠራዊቱ ትልቅ ለውጥ እያመጣ ነው ባይ ናቸው፡፡ በማስረጃነትም በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና በመስኖ ልማት የመጡትን ለውጦች ይጠቅሳሉ፡፡ እነዚህ ለውጦች ዝም ብለው የመጡ ሳይሆን ህዝቡና የመንግስት አደረጃጀቶች ተቀናጅተው ያመጧቸው እንደሆኑ በአጽንኦት የሚገልፁት ሃላፊው፤ በ1 ለ5 አደረጃጀት ውስጥ የሚሳተፍ ሁሉ የኢህአዴግ አባል ነው ማለት አይደለም ይላሉ፡፡  “የኢህአዴግ አደረጃጀት የተለየ ነው፡፡ ከላይ ጀምሮ መሠረታዊ ድርጅት፣ ህዋስ እያለ እስከታች ይወርዳል፡፡ ይሄኛው ግን የተቃዋሚ ደጋፊና አባል ጭምር የሚሳተፍበት የመላው ህዝብ አደረጃጀት ነው፡፡ የተቃዋሚ አባል በመሆኑ በአደረጃጀቱ አትገባም አይባልም” የሚሉት አቶ ደስታ፤ የኢህአዴግ አባል የሆኑትም  ከድርጅቱ መዋቅር ባሻገር በዚህ አደረጃጀት ውስጥም መሳተፍ ይችላሉ ብለዋል፡፡
የ1 ለ5 አደረጃጀት የኢህአዴግ አባላት ብቻ የተደራጁበት ነው ተብሎ የሚገለፀው ስህተት ነው ያሉት አቶ ደስታ፤ ለልማት ህዝቡ ቢደራጅ ምንድን ነው ክፋቱ ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡ ኢህአዴግ አደረጃጀቱን ለምርጫ ይጠቀማል የተባለውም የሃሰት ውንጀላ ነው የሚሉት ሃላፊው፤ ”ምርጫ የህዝብ ጉዳይ ነው፣ ነገር ግን ምርጫው ሠላማዊና ፍትሐዊ እንዲሆን፣ ለምርጫ ምዝገባና ተሳትፎ ህዝብ እንዲወጣ ለማድረግ ተመሳሳይ አደረጃጀቶችን መጠቀም ሃጢያት አይደለም፣ ህዝብ የሚመርጠው ግን የሚቀርብለትን የፖሊሲ አማራጭ መሠረት አድርጐ ነው” ብለዋል፡፡ 

“መሣሣት የሰው ነው፡፡ ይቅር ማለት ግን የመለኮት!”
(to err is human, to forgive is divine)
ሁለት ሰዎች ከሩቅ አንድ የአውሬ ቅርፅ ያያሉ፡፡
አንደኛው፤
    “ያ የምናየው እኮ ጅብ ነው” አለ፡፡
ሁለተኛው
    “ያ የምናየው እኮ አሞራ ነው” አለ፡፡
አንደኛው፤
    “እንወራረድ?”
ሁለተኛው፤
    “በፈለከው እንወራረድ!”
አንደኛው፤
    “እኔ አንድ በቅሎ አገባ!”
ሁለተኛው
    “እኔም በቅሎ ከነመረሻቷ አገባ!”
መልካም፡፡ ቀረብ ብለን እንየው፡፡ እየተጠጉ መጡ፡፡
አንደኛው፤
    “አሁንም በአቋምህ ፀንተሃል? አሞራ ነው የምትል?”
ሁለተኛው፤
    “ከፈራህ አንተ አቋምህን ቀይር እንጂ እኔ አሞራ ነው ብያለሁ አሞራ ነው!”
አንደኛው፤
    “እኔ ፈሪ ብሆን ጅብ መሆኑን እያየሁ ቀርበን እናረጋግጥ እልሃለሁ?!” አለ በቁጣ፡፡
እየቀረቡ መጡ፡፡
የእንስሳው ቅርፅ አሁንም አልተለየም፡፡
ተያይዘው ቀረቡ፡፡
እጅግ እየተጠጉ ሲመጡ፤ ያ ያዩት እንስሳ አሞራ ኖሮ ተነስቶ በረረ፡፡
ሁለተኛው ሰው፤
    “ይኼው በረረ፡፡ አሞራነቱ ተረጋግጧል፤ ተበልተሃል!”
አንደኛው፤
    “በጭራሽ አልተበላሁም!”
ሁለተኛው፤
    “እንዴት? ለምን? አስረዳኛ?!”
ይሄኔ አንደኛው፤
    “ቢበርም ጅብ ነው! መብረር የሚችል ጅብ መኖር አለመኖሩን በምን ታውቃለህ? አለው፡፡”
                                            *     *      *
በህይወታችን ውስጥ የዋሸነው፣ የካድነውና በዕንቢ-ባይ ግትርነት አንቀበለውም ያልነው፤ በርካታ ነገር አለ፡፡ የሁሉ ቁልፍ፤ ስህተትን አምኖ፣ ተቀብሎ ራስን ለማረም ዝግጁ መሆን ነው!!
ይቅርታ መጠየቅና ይቅር ማለት የዘመኑ ምርጥ አጀንዳ ነው - በተለይ በኢትዮጵያ - በተለይ በዳግማይ ትንሣኤ ሰሞን! ሰሞኑን “በአይዶል” ፕሮግራም በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ያየናት ልጅ፤ ከፋሲካ እስከ ዳግማይ ትንሣዔ ብሎም እስካገራችን ዕውነተኛ ትንሣዔ ድረስ፣ ከተማርን ከተመካከርንባት፣ ልዩ ተምሣሌት፣ ልዩ አርአያ ናት፡፡ “መሣሣት የሰው ነው፤ ይቅር ማለት ግን የመለኮት” የሚለው አባባል ትርጓሜው” እዚህ ጋ ይመጣል፡፡ የዋሸነውን፣ ለማታለል ያደረግነውን ለማሳመን መንገዱ ይሄ ነው ብለን ሰው ሁሉ/ ህዝብ ሁሉ እንዲያምነን ላደረግነው ነገር፤ ቆይተን፣ ተፀፅተን፣ ለራሳችን ህሊና ተገዝተን፣ ንሥሐ መግባት መልመድን የመሰለ መንፈሣዊ አብዮት የለም፡፡ ያን መሣይ መንፈሣዊ ለውጥ አይገኝም!! እስከዛሬ፤ በቀደሙትም ሆነ አሁን ባሉት ፓርቲዎች ዘንድ፣ በቀደሙት መንግሥታትም፣ አሁን ባለው መንግሥትም ዘንድ የማይታወቀው፤ እጅግ ቁልፍ ነገር፤ “ተሳስቻለሁ… ይቅርታ” ማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ያየናት የ“አይዶል” ተወዳዳሪ ድምፃዊት ያሳየችንና ያስተማረችን ጉዳይ ይሄው ነው፡፡ በእኛ ግንዛቤ፤ ተወዳዳሪዋ በድምፃዊ አረጋኸኝ ወራሽ ቤት በልጅነቷ በቤት ሠራተኝነት ተቀጥራ፣ ቀጣሪውን ማለትም አርቲስቱን ስለራሷ ህይወት ዋሽታዋለች፡፡ አርቲስቱ በሰማው አሳዛኝ የህይወት ታሪክ ልቡ ተነክቷል፡፡ ትምህርት እንድትጀምርም ያደርጋል፡፡ ልጅቱ ድንገት ከቤት ትጠፋለች፡፡
ዛሬ ግን አርቲስቱ በዳኝነት በተገኘበት መድረክ፤ የ“አይዶል” ድምፃዊት ተፈታኝ ሆና ስትቀርብ ድምጿን ካሰማች በኋላ፤ “ከመዳኘቱ በፊት አንድ ነገር ለመናገር እፈልጋለሁ አለች፡፡” ዳኞቹ ፀጥ አሉ፡፡
እዚህ መካከል አንድ የማውቀው ሰው አለ፡፡ እሱም ግር ብሎት ካልሆነ ያውቀኛል፡፡ እሱ ቤት በልጅነቴ ተቀጥሬ ነበር፡፡ ሁኔታዬንና የውሸት ታሪኬን ሰምቶ፤ አምኖኝ፣ ት/ቤት አስገብቶኝ፤ እኔ ግን ከቤቱ ጠፍቼ ሄጃለሁ፡፡ ያ ሰው፤ ድምፃዊ አረጋኸኝ ወራሽ ነው… እሱ ቤተሰቦቼን ሊያፈላልግ ሞክሯል ግን አልተሳካለትም፡፡
“እኔም ተመልሼ ሁኔታውን ለመግለጽ ሁኔታውም ድፍረቱም አልነበረኝም፡፡” የምትለው አርቲስት፤ “ዛሬ ግን ዕውነቱን ለማሳወቅ እፈልጋለሁ፡፡ ስለቤተሰቦቼ አለመኖርና ስራ ስለማጣቴ ሁሉ ያወራሁት ውሸት መሆኑን ዛሬ በግልጽ ማስረዳት እፈልጋለሁ፤ ይቅርታ እንዲያደርግልኝም እጠይቃለሁ” ነው የንሥሐዋ መንፈስ! የዳግማይ ትንሣዔ መሪ መልዕክት (1) “ልናጠፋ እንችላለን ግን ይቅርታ ጠይቀን ቀሪውን ህይወት ማስተካከል እንችላለን” ነው፡፡ ልብ እንበል፤ ልጅቱ ለአረጋኸኝ ወራሽ ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያ ህዝብ ነው ንሥሐዋን የተናገረችው! አቤት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ይሄን ቢያውቁ! አቤት ገዢው ፓርቲ ይሄን ቢችልበት አቤት በየደረጃው ይቅርታ መጠየቅ አልባ የሆነ ኃላፊ፣ አለቃ እና የበላይ ይህን ቢረዳ! አቤት አበሻ በጠቅላላ፤ ይሄ ቢገባው!
ሁለተኛው የፋሲካና የዳግማይ ትንሣዔ ግብረገባዊ ትምህርት (The Moral of the Story) የ “ጆሲ ኢን ዘ ሐውስ” ገድል ነው፡፡ የማን ያለብሽ ዲቦን ልጆችና እህት አንድ መጠለያ ለማስገኘት ጆሲ ያረገው ጥረት የወቅቱ መልዕክት ነው፡፡
ትምህርት 1) ከኢትዮጵያ የቤት - ነክ ቢሮክራሲ ጋር፣ ውጣ ውረዱን ችሎ፣ ታግሦ፣ ተቻችሎ ውጤት ማስገኘት
ትምህርት 2) እያንዳንዱን ክስተት በካሜራ ቀርፆ፣ መንግሥትም አምኖበት ለዕይታ መብቃቱ፤
ትምህርት 3) የመንግሥት ፈቃደኝነትና አዎንታዊ እርምጃዎች መረጋገጥ
ትምህርት 4) በየደረጃው ያሉ ስፖንሰሮች ሀ) የደብረዘይት መናፈሻ ቦታው ስፖንሰርሺፕ ለ)የመጓጓዣ መኪናው  ሐ) የአዋሳ ኮሜዲያን መምጣት መ) የጋሽ አበራ ሞላ መምጣት ሠ)የቤት - ዕደሳ ላይ የተሳተፉት ስፖንሰር ድርጅቶች መኖር ረ) የቤት ዕቃዎች ለማሟላት አስተዋጽኦ ያደረጉ ስፖንሰሮች መኖር ሰ) ለልጆቹ ትምህርት መቀጠል የት/ቤቶችና የዩኒቨርሲቲዎች ትብብር፣ ሸ) የኮምፒዩተር እገዛ ለማድረግ የተባበሩ ኮምፒዩተር አስመጪዎች     
ትምህርት 5) የልጆቹ መኖሪያ ጐረቤቶችን ማሰባሰብና ጉዳዩን እንዲረዱ ማድረግ፣ ሰው                   የአካባቢው ውጤት መሆኑን ይነግረናል፡፡
እኒህን ሁሉ ስፖንሰሮችና ነዋሪዎች አስተባብሮ ዓይነተኛና አርአያዊ ተግባር መፈፀሙ ጆሲን ድንቅ የሚያሰኘው ነው፡፡ ማስታወቂያ ሰሪዎች እንማር! አገር አልሚዎች እንማር! የተቀደሰ ተግባር፣ ለተቀደሰ ትንሣኤ እንደሚያበቃን ለማረጋገጥ የጆሲ ዚን ዘ ሐውስን ተምሳሌትነት እንገንዘብ፡፡ አንድ ቤተሰብ መገንባት ሙሉ አገር መገንባት ነው፤ “አምሣ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክሙ ለአምሣ ሰው ጌጡ ነው” ነው መንፈሱ፡፡ በርካታ ስፖንሰሮች ለመዝናኛ ስፖንሰር እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ ይመሰገናሉም፡፡ ሆኖም ዛሬ የተሻለ ስፖንሰራዊ ተግባር አይተናል፡፡ በየማስታወቂያዎች ውስጥ መዝናኛ ብቻ ሳይሆን ቁምነገር፣ ለሀገር የሚጠቅም ጉዳይ፣ መካተት እንደሚችል በአጽንኦት ይጠቁመናል፡፡ ለብዙዎቻችን ትምህርት ነው፡፡ ሁሉን አቀፍ የስፖንሰርሺፕ እንቅስቃሴ አገር ያለማል፡፡ እንደ ጆሲ ያለ ልባዊና ልባም ሥራ ምን መምሰል እንዳለበት ታላቅ ደርዝ፣ ታላቅ ፍሬ - ጉዳይ ያስጨብጠናል፡፡ አገር የሚመራ ይህን ይገንዘብ፣ ማስታወቂያ የሚሠራ ይሄን ይገንዘብ፤ አገርን የሚያስብ ይሄን ይገንዘብ፡፡ “መልካም ሥራ ሥራና ሠይጣን ይፈር” የሚለው የሼክስፒር ጥቅስ ትልቅ ትርጉም የሚኖረው ዛሬና እዚህ ላይ ነው!!

Published in ርዕሰ አንቀፅ
Saturday, 26 April 2014 12:16

እኔ ተጎድቼ

ትዝ ይልሻል ውዴ ሆዴ፣
አንቺ የልቤ ሁዳዴ!
ፆም እንያዝ ተባብለን
እንዳቅማችን ተሟሙተን
አንድ ሆቴል “በልተን ጠጥተን”
“ቦዩን አልጋ አለ ወይ?” ብለን
ትዝ ይልሻል ምን እንዳለን?
“ይቀልዳሉ እንዴ ጋሼ?
እንኳን አልጋው ይቅርና
ጨለማው ተይዟልኮ!” አለን፡፡
ዕውነትም ዙሪያውን ብናይ፤
ጨለማው በመኪና ሞልቶ
መኪናው በጥንዶች ትንፋሽ፣ የፍቅር ምጥ ሳግ አግቶ
ዕውር ጨለማ በዕውር ሰው፣ ፆም እየያዘ ነው ተግቶ!
በመቀደማችን ነዶን
ከወሲብ ጦሩ ራቅ እንዳልን
እንዳቅሜ አበባ ሸልሜ፣ ለፆም መያዣሽ ሰጠሁሽ
የፆም መያዣ ቀለበት፣ በጣትሽ ላይ አሰርኩልሽ
በወርቅ ይሁን ባርቲፊሻል፣ ፆም ከያዝሽ ምን ቸገረሽ!!
የፆም መያዣ ፍቅር፣ ጭፈራውን ጋብዤሻለሁ
በቃ አለቀ ውዴ ሆይ! ፆም ይዘሻል፤ ፆም ይዣለሁ!
እግረ መንገዳችንንም፡- ሥጋ መግዛቱን ፆመናል
ቅቤ ማሽተትን ገድፈናል
ዶሮን ከነባልትናዋ፣ በሰላም ተገላግለናል
“እንዳካሄድ” ሳስበው፣
የኢኮኖሚያችን መፍትሔ፣ በርትቶ ፆምን መያዝ ነው፡፡

ዛሬ ደግሞ እዚህ ደረስን፣ ሥጋ መቼም ያው ሥጋ ነው
በእኔው ቆርጠሸ ብትፈስኪ፣ ብትፀድቂ ነው እሚሻለው!
የፆመ ባልፆመ አጣማጅ፣ ከፈሰከ ፋሲካ ነው፡፡
ከሁለት ወር ቆይታ ዳር፣ ደሞ ዛሬ ስንገናኝ
በሬው ፆሟል፣ እኔ አልፆምኩም፤ ብዙው የፍስክ እኔ ነኝ
አንቺ ውስጥ የከረምኩትን፣ ዕውን ረስተሸኝ ከሆነ
አዲስ ፋሲካ አግኝተሻል፣ በአካል በነብስ የዘበነ!!
እናም ያልፆምኩት ላንቺው ነው፣ ፍስክ ገላ ሆኜ እንድገኝ
ባልፆመ ሥጋ ፈስከሽ፣ ከልብሽ እንድትፀድቂልኝ፡፡
አንቺም አንቺን ሰጥተሽኛል፣ እኔም እኔን ሰጥቻለሁ፤
አንቺም በእኔ ፈስከሻል፣ እኔም ባንቺ ፆም ይዣለሁ!!
ምንም ትርጉሙ ባይገባኝ፣ “ፆም ማኪያቶ” እንደሚሉት
ፍቅርም ማኪያቶ አያጣ፤ ቢያንስ ባይን የሚገበዩት!
ይህንን ብጠራጠርም
ዕውን ከፆምሽ ፈስኪብኝ
ሥጋ ለሥጋ የሄደ፣ ጥይት አይጎዳም ይላሉና፤
እኔስ አላንቺ ማን አለኝ፡፡
ባንቺ ልፅደቅ በቃ ሆዴ፣ አንቺም በኔ ፅደቂብኝ፡፡
“እኔ ተጎድቼ! ይላል፣ ያገሬ ነጋዴ ሲቀኝ!
በቃ “እኔ ተጎድቼ”፣ በመጣሁበት ውሰጂኝ”!!
(ለፆም መያዣ እና ለፍስክ ፍቅረኞች)
                        በ2006 ሁዳዴ ፆም መያዣ ተጀምሮ
በህማማቱ አለቀ

Published in የግጥም ጥግ

 በግድቡ ላይ ለሚከሰት አደጋ፣ ሙሉ ለሙሉ ተጠያቂ የማደርገው ግብጽን ነው ብላለች - ሱዳን
“በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጽኑ እምነት አለን፣ የገንዘብ ጉዳይ አያሰጋንም!” - ሳሊኒ ኮንስትራክሽን

ግብፅ ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ አለማቀፍ የገንዘብ ብድሮች፣ ከውጭ መንግስታት እንዳይገኙ በማድረግ ግንባታውን ለማደናቀፍ እያሴረች ነው ስትል ሱዳን አወገዘች፡፡
የሱዳን ምስራቃዊ ብሉ ናይል ግዛት ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት ሁሴን አህመድ፣ ኢትዮጵያ በማከናወን ላይ ለምትገኘው የታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ የሚውሉ አለማቀፍ ብድሮችን እንዳታገኝ ለማድረግ በግብጽ በኩል በድብቅ እየተከናወኑ ያሉት አግባብ ያልሆኑ ተግባራት፣ ግድቡ በገንዘብ እጥረት ሳቢያ ከሚፈለገው የጥራት ደረጃ በታች እንዲሰራና ለአደጋ እንዲጋለጥ ሊያደርጉ ይችላሉ በማለት ድርጊቱን ማውገዛቸውን ሱማሌላንድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
ግድቡ ከሚፈለገው የግንባታ ጥራት በታች የሚሰራ ከሆነ፣ በረጅም ጊዜ ሂደት የሚፈርስበት ዕድል እንደሚኖርና ተያይዞ የሚከሰተው የጎርፍ አደጋም ሱዳንን ክፉኛ ሊጎዳ የሚችል በመሆኑ፣ ሱዳን የግብጽን ድርጊት አጥብቃ እንደምትቃወመውና ለሚደርሰው አደጋ ሙሉ በሙሉ ተጠያቂ እንደምታደርጋት ባለስልጣኑ መናገራቸውን ዘገባው ያስረዳል፡፡
የሱዳን ምስራቃዊ ብሉ ናይል ግዛት፣ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ከሚከናወንባት የቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልሏ ጉባ ጋር በቅርብ ርቀት የሚካለል እንደመሆኑ፣ በግድቡ ላይ የመፍረስ አደጋ ቢከሰት፣ ግዛቱ በጎርፍ አደጋ ሙሉ ለሙሉ ሊወድም እንደሚችል ባለሙያዎች የሰጡትን አስተያየት ያቀረበው ዘገባው፣ ይህም የግዛቱን ባለስልጣናት እንዳሳሰባቸው ጠቁሟል፡፡
ግብጽ በግድቡ ላይ ባለቤትነት እንዲኖራት እንጂ፣ ስለ አካባቢው ደህንነት ደንታ የላትም ያሉት ባለስልጣኑ፣ የግድቡን ግንባታ በራሷ ወጪ ለማከናወንና በበላይነት ለማስተዳደር ከመጀመሪያ አንስቶ ፍላጎት እንደነበራት ተናግረዋል፡፡
“በግንባታ ጥራት መጓደል ሰበብ በግድቡ ላይ ለሚፈጠር የመፍረስ አደጋና ከዚያ ጋር ተያይዞ በግዛታችን ላይ ለሚከሰት የጎርፍ አደጋ፣ ሱዳን ሙሉ ለሙሉ ተጠያቂ የምታደርገው ግብጽን ነው” ያሉት ባለስልጣኑ፣ ግብጽ አስር አገራት በጋራ በሚጠቀሙበት የአባይ ወንዝ ላይ ኢኮኖሚዋን ሙሉ ለሙሉ ጥገኛ ከማድረግ ይልቅ፣ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዋን በሌሎች መስኮችም ማስፋፋት እንደሚኖርባት ተናግረዋል፡፡
ግብጽ ከረጅም አመታት በፊት የገነባችው አስዋን ግድብ፣ የኑብያ ህዝቦችን ህልውና ክፉኛ መጉዳቱንና ጥንታዊ የዕደ-ጥበብ ስራዎችን ማውደሙን ያስታወሱት ባለስልጣኑ፣ ይሄም ሆኖ ግን የትኛውም አገር የግድቡን ግንባታ እንዳልተቃወመና ስራዋን ለማደናቀፍ እንዳልሞከረ ገልጸዋል፡፡
የሱዳኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ ካርቲም፣ ባለፈው ጥቅምት ወር ግብጽ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላይ ያነሳችውን ተቃውሞ እንደተቹት የጠቀሰው ዘገባው፣ ሚኒስትሩ በተለይም የግብጽ መገናኛ ብዙሃን ግድቡን በተመለከተ መሰረተ ቢስ መረጃዎችን እያናፈሱ ነው በማለት መክሰሳቸውንና የግድቡ መገንባት ሊያስከትላቸው ይችላሉ ተብለው ከሚጠቀሱ ማናቸውም አይነት ችግሮች ይልቅ፣ ጠቀሜታው እጅግ የጎላ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው መናገራቸውን አስታውሷል፡፡
ተቀማጭነቱ በአውሮፓ የሆነው ስቶክሆልም ኢንተርናሽናል ዋተር ኢንስቲትዩት የተባለ አለማቀፍ ተቋም፣ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መገንባት፣ ግብጽ ለደለል ቁጥጥርና በትነት ሳቢያ የሚጠፋውን ውሃ ለማስቀረት ታወጣው የነበረውን በሚሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር ገንዘብ የሚያስቀርላት በመሆኑ፣ ለኢትዮጵያ ገንዘብ መክፈል ይገባታል ማለቱንም ዘገባው ጨምሮ አስታውሷል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት፣ በዜጎቹ የገንዘብ መዋጮ የተጀመረው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ፣ በተያዘለት ዕቅድ መሰረት ግንባታው እየተከናወነ እንደሚገኝ፣ ከግድቡ ግንባታ ጋር በተያያዘ የገንዘብ ችግር እንደማይገጥመውና በታሰበው የጥራት ደረጃና በተያዘለት የጊዜ ገደብ ተሰርቶ እንደሚጠናቀቅ በተደጋጋሚ መግለጹ ይታወቃል፡፡
የሮይተርስ ዘጋቢ አሮን ማሾ በበኩሉ፣ የታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በማከናወን ላይ የሚገኘው ግንባር ቀደሙ የጣሊያን ኮንስትራክሽን ኩባንያ ሳሊኒ፣ ከግንባታው ጋር የተያያዙ ክፍያዎች በሙሉ በወቅቱ እየተፈጸሙለት እንደሆነ  ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
የኮንስትራክሽን ኩባንያው፣ የኢትዮጵያ መንግስት በቀጣይም የግድቡን ግንባታ ለማጠናቀቅ የሚያስፈልገውን በቢሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር ቀሪ ገንዘብ በማሟላት ረገድ፣ ችግር ይገጥመኛል ብሎ እንደማያስብና ከፋይናንስ እጥረት ጋር በተያያዘ ምንም አይነት የሚያሰጋው ነገር እንደሌለ መናገሩን የሮይተርስ ዘገባ ጨምሮ ገልጧል፡፡ “በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጽኑ እምነት አለን፣ የገንዘብ ጉዳይ አያሰጋንም!” ብሏል ሳሊኒ ለሮይተርስ፡፡

Published in ዜና

“ቦርድ” ለሚወጡ ወታደሮች የ2 በመቶ ክፍያ ተጨመረ

የመከላከያ ሚኒስቴር እንደአስፈላጊነቱ እያየ የጦር መኮንኖችን የአገልግሎት ዘመንና የጡረታ መሰናበቻ እድሜ በሁለት ዓመት ለማራዘም የነበረው ሥልጣን እንደተሻሻለ ምንጮች ገለፁ፡፡ የመከላከያ ኃይል አባላት የሥራ ዘመናቸውን በ3 ወይም በ5 ዓመት ማራዘም በአዲሱ አሰራር ተፈቅዷል፡፡ የጡረታ እድሜ በ5 ዓመት የሚራዘመው ለከፍተኛ መኮንኖች እንደሆነ ምንጮች ጠቅሰው፤ ከከፍተኛ መኮንን በታች ደግሞ ካሁን ቀደም የነበረው የሁለት ዓመት ማራዘሚያ ወደ ሶስት አመት ከፍ እንዲል መደረጉን ገልፀዋል፡፡
ከዚሁ የጡረታ ማራዘምያ አዲስ አሰራር ጋር፤በ“ቦርድ” ለሚሰናበቱ የመከላከያ ኃይል አባላት የሁለት በመቶ ክፍያ ተጨምሯል፡፡ የመከላከያ ሠራዊት አባል በተለያዩ ምክንያቶች “ቦርድ” እንዲወጣ ሲወሰን፣ ወርሃዊ ክፍያው የደሞዙ አርባ አምስት በመቶ የነበረ ሲሆን አሁን አርባ ሰባት በመቶ እንዲሆን ተወስኗል፡፡

Published in ዜና

የፌደራል ባለስልጣናት ጣልቃ ገብተው ሲያረጋጉ ሰንብተዋል

የድሬደዋ ዩኒቨርስቲ የሶማሌ ክልል መስተዳድር የባለቤትነት ጥያቄ ተነስቶበት ካለፈው ቅዳሜ ጀምሮ በሚሊሻ ተቆጣጥሮት የነበረ ሲሆን የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተ/ማርያም፣ የቀድሞ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ አዲሱ ለገሠ፣ የግብርና ሚኒስትሩ አቶ ተፈራ ደርበውን ጨምሮ ሌሎች የፌደራል ባለስልጣናት በጉዳዩ ጣልቃ ገብተው ማረጋጋታቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የዩኒቨርስቲው ባለቤት እኔ ነኝ የሚል ጥያቄ ያነሣው ሶማሌ ክልል ቦታውን በክልሉ ሚሊሻዎች አስከብቦ የክልሉን ባንዲራ ሰቅሎ የነበረ ሲሆን፣ የፌደራል ባለስልጣናቱ በጉዳዩ ጣልቃ መግባታቸውን ተከትሎ ክልሉ ሐሙስ እለት ሚሊሻዎቹን ከአካባቢው ቢያስወጣም የክልሉ ባንዲራ አሁንም በዩኒቨርስቲው አካባቢ እየተውለበለበ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
የድሬደዋ ዩኒቨርስቲ የሚገኘው በድሬደዋ አስተዳደር በኩል “ቀበሌ 02” ተብሎ የሚጠራ ሲሆን፤ የሶማሌ ክልል መስተዳድር በበኩሉ፤ ዩኒቨርስቲው አጠገብ “በሶማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ቦረን ገጠር አስተዳደር” የሚል ታፔላ እንደተከለ ምንጮች ገልፀዋል፡፡ በአካባቢው የሚገኙ መኖሪያ ቤቶችም ባለሁለት ካርታ መሆናቸውን የገለፁት ነዋሪዎች፣ በሶማሌ ክልል እና በድሬደዋ ከተማ አስተዳደር ካርታ የወጣላቸው እንደሆኑ ጠቁመዋል፡፡ እንዲሁም ዩኒቨርስቲው ጀርባ የሚገኙ ገበሬዎች ባነሱት የመሬት ጥያቄ ምክንያት ያለ አጥር ክፍቱን የተቀመጠ መሆኑንም ምንጮች ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

እስካሁን 5.2 ሚሊዮን ብር ወጥቶበታል ተብሏል

በ“አውሮራ ኤቨንትስ ኦርጋናይዘር” አዘጋጅነት ዛሬ በሚሌኒየም አዳራሽ ሊካሄድ ታቅዶ የነበረው “ሬጌ ዳንስሆል ኢን ኢትዮጵያ ቁጥር አንድ” የሙዚቃ ድግስ ላልተወሰነ ጊዜ መራዘሙን አዘጋጆቹ ገለፁ፡፡ ኮንሰርቱ የተራዘመው ዛሬ ምሽት በጊዮን ሆቴል ከሚቀርበው የአርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) “ወደ ፍቅር ጉዞ”  የሙዚቃ ድግስ ጋር መደራረብ እንዳይፈጠር ታስቦ እንደሆነ አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡
የ“አውሮራ ኤቨንትስ ኦርጋናይዘር” ስራ አስኪያጆች ከትናንት በስቲያ ከሰዓት በኋላ በሚሌኒየም አዳራሽ በሰጡት መግለጫ እንዳስታወቁት፤ ኮንሰርቱ መራዘሙ እስከተወሰነበት ጊዜ ድረስ ለዝግጅቱ 5.2 ሚሊዮን ብር ወጪ ተደርጓል፡፡ አዘጋጆቹ ለኮንሰርቱ መራዘም የቴዲ አፍሮን የሙዚቃ ድግስ እንደ ምክንያት ቢያቀርቡም ምንጮች እንደሚሉት፤ በኮንሰርቱ ላይ ይዘፍናል የተባለው ጃማይካዊው ድምፃዊ ቢዚ ሲግናል ወደ ኢትዮጵያ መምጣት ባለመቻሉ ነው፡፡ ጃማይካዊው ዘፋኝ ባለው የፀረ ተመሣሣይ ፆታ አቋሙ የተነሳ እንግሊዝ፣ አሜሪካ እና ካናዳ ወደ አገራቸው እንዳይገባ ከልክለውታል የሚሉት ምንጮች፤  የሚመጣበት አውሮፕላን ደግሞ ከጃማይካ ተነስቶ እንግሊዝና አሜሪካ የሚያርፍ በመሆኑ በበረራ ችግር  ማምጣት አለመቻሉን ጠቁመዋል፡፡
አርቲስት ቢዚ ሲግናል፤ በዚህ አቋሙ የተነሳ አሜሪካ፣ እንግሊዝና ካናዳ እንዳይገባ መከልከሉን ያመኑት የኮንሰርቱ አዘጋጆች፤ኮንሰርቱ የተራዘመው ግን ፈፅሞ በዚህ ምክንያት አይደለም ሲሉ አስተባብለዋል፡፡ “ሬጌ ዳንስሆል ኢን ኢትዮጵያ ቁጥር አንድ” የሙዚቃ ድግስ ላልተወሰነ ጊዜ የተራዘመበት ዋነኛ ምክንያት፣ “በአዲስ አበባ ከሚኖረው አራት ሚሊዮን ህዝብ ውስጥ ለኢንተርቴይንመንት ፍቅር ያለው ጥቂቱ ሲሆን ከእዚህም ውስጥ ሁለት ቦታ ተከፍሎ የሚመጣው አመርቂ አይሆንም ብለን በማመናችን ነው” በማለት በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡
ኮንሰርቱ ለመቼ እንደተራዘመ የተጠየቁት አዘጋጆቹ፤ ከሶስት ቀናት በኋላ ይሄንኑ ለማሳወቅ ሌላ ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጡ ተናግረዋል፡፡ ይህን ፕሮግራም ስታቅዱ ቴዲ አፍሮ ኮንሰርት እንዳለው አታውቁም ነበር ወይ? በሚል ለተነሳላቸው ጥያቄም “በእርግጥ እናውቃለን፤ነገር ግን ከዚያ በኋላ ባደረግነው ጥናት፣ ወደ ድግሱ የሚመጣው ህዝብ ሁለት ቦታ ሊከፋፈል አይገባም፤ አውሮራ ኤቨንትስ የሚያዘጋጀው ኮንሰርትም ብራንድ አይደንቲቲው መጠበቅ አለበት በሚል ለተከታታይ ሶስት ቀናት ከፍተኛ ውይይትና ምክክር ከተደረገ በኋላ እንዲራዘም ተደርጓል” ብለዋል አዘጋጆቹ፡፡
በተለይ አርቲስት ቢዚ ሲግናል፣ሶስት አገሮች እንዳይገባ ከመከልከሉ ጋር ተያይዞ ከአዲስ አድማስ ለተነሳው ጥያቄ አዘጋጆቹ ሲመልሱ፣ “አርቲስቱ እንዳይገባ የተደረገው እንግሊዝ፣ አሜሪካና ካናዳ ብቻ ስለሆነ ከጃማይካ ቱርክ፣ከቱርክ ፍራንክፈርት፣ ከዚያ አዲስ አበባ መምጣት ይችል ነበር ካሉ በኋላ ዋናው ትኩረታችን የኮንሰርቱ መደራረብ ስለሆነ፣ ተመካክረን እስክንወስን ትኬት መሸጥ እንኳን አልጀመርንም ነበር ብለዋል፡፡
ኮንሰርቱ በመራዘሙ ለአርቲስት ቢዚ ሲግናል፣ቀደም ሲል ከተከፈለው የ10 በመቶ ጭማሪ ክፍያ ማድረጋቸውንም አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

     ፊሊንትስቶን ኢንጂነሪንግ ኩባንያ፤ በአንድ ህንፃ ላይ ለበርካታ አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች አገልግሎት መስጠት ያስችላል ያለውን አዲስ ፕሮጀክት ይፋ ያደረገ ሲሆን የመጀመሪያው ባለ 8 ፎቅ ህንፃ በቅርቡ ጎተራ ማሳለጫ አካባቢ ግንባታው ይጀመራል፡፡
ከአንድ ዓመት በላይ በፈጀ ጥናት የአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችን ችግርና የእድገት ማነቆዎች መገንዘብ ችለናል ያሉት የኩባንያው ምክትል ኃላፊ አቶ ብሩክ ሽመልስ፤ የኢንተርፕራይዞቹ ዋነኛ ችግሮች በተመጣጣኝ ዋጋ የማምረቻ ቦታ ባለቤት ለመሆን አለመቻልና የገንዘብ እጥረት መሆኑን ጥናቱ አረጋግጧል ብለዋል፡፡ በተመጣጣኝ ዋጋ የሚቀርቡ የማምረቻ ቦታዎችን የግል አድርጎ ለመጠቀም  ከፍተኛ ፍላጎት እንዳለ በኮልፌ፣ መርካቶ እና አውቶብስ ተራ አካባቢ በሚገኙት አምራቾች ላይ በተደረገው ጥናት መረጋገጡንም ኃላፊው ገልፀዋል፡፡
በአንድ ህንፃ ላይ በርካታ ኢንተርፕራይዞች የማምረቻ እና የመሸጫ ቦታዎች ባለቤት ማድረግ ያስችላል የተባለው ይህ ፕሮጀክት፤ ግንቦት 9 ቀን 2006 ዓ.ም ጎተራ ማሳለጫ አካባቢ ለሚገነባው ባለ 8 ፎቅ ህንፃ የመሰረት ድንጋይ በመጣል የሚጀመር ሲሆን በቀጣይም በሌሎች የተጠኑ የከተማዋ አካባቢዎች ተመሳሳይ ህንፃዎች ይገነባሉ ተብሏል፡፡
ጎተራ ማሳለጫ አካባቢ የሚገነባው የመጀመሪያው ህንፃ፤ 134 ለሚሆኑ የቆዳና የቆዳ ውጤቶች፣ የጫማ፣ የጨርቃጨርቅ ስፌት እና የማተሚያ ቤት ኢንተርፕራይዞች የሚውል ሲሆን የማሽነሪና ሌሎች ወጪዎችን ጨምሮ ወደ 98 ሚሊዮን ብር ገደማ በጀት ተይዞለታል፡፡ ህንፃው ከሁለት እስከ ሦስት ዓመታት ባሉት ጊዜያት ውስጥ ተጠናቆ ለተጠቃሚዎች ይተላለፋል ብለዋል ኃላፊው፡፡
ለህንፃው ከተያዘው አጠቃላይ በጀት 10 በመቶ የሚሆነው ለማሽነሪዎች ግዢ የሚውል ሲሆን ደንበኞች የማምረቻ ክፍሎቹን ከተረከቡ በኋላ በኩባንያው የተተከሉን ማሽነሪዎች የማይፈልጓቸው ከሆነ የራሳቸውን ማሽን ማስተከል ይችላሉ ተብሏል፡
የአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችን አቅም ያገናዘበ ነው የተባለው ይህ ፕሮጀክት ከ12 እስከ 40 ካሬ ሜትር የሚደርስ ስፋት ያላቸው ክፍሎች ሲኖሩት እንደየ ኢንዱስትሪዎቹ የሰው ፍላጎት ከ4 እስከ 12 ሰራተኞችን ማካተት ይችላሉ፡፡ የዚህ ፕሮጀክት ተጠቃሚ ይሆናሉ ተብለው የታሰቡትም በአማካይ ከግማሽ እስከ 1 ሚሊዮን የሚደርስ መነሻ ካፒታል ያላቸው ሲሆኑ ክፍሎቹም ከ650 ሺህ ብር ጀምሮ በተቆጠረ ዋጋ ለሽያጭ ይቀርባሉ ተብሏል፡፡ ከ23 ዓመት በፊት የተቋቋመው ፊሊንትስቶን ኢንጅነሪንግ በተለያዩ የአዲስ አበባ አካባቢዎች የመኖሪያ ቤቶችን በዝቅተኛ ዋጋ ገንብቶ በመሸጥ ይታወቃል፡፡   

Published in ዜና

ከኦጋዴን ብሄራዊ ነፃ አውጪ ግንባር (ኦብነግ) ጋር ለሽብር ተልዕኮ ሲንቀሳቀሱ ነበር በሚል በቁጥጥር ስር ውለው የተፈረደባቸውን ሁለቱን የስዊድን ጋዜጠኞች በይቅርታ ለማስፈታት ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር የተደረገውን ድርድር እና አጠቃላይ ሂደት የሚያትት መፅሐፍ በቀድሞው የስዊድን አምባሳደር ተዘጋጅቶ  ለንባብ በቃ፡፡
ለ4 ዓመታት በኢትዮጵያ የስውዲን አምባሳደር በነበሩት ዮስ ቡድላንደር የተፃፈው “ዲፕሎማሲ” የተሰኘው መፅሃፍ፤የሁለቱ ጋዜጠኞች ጉዳይ እንዴት ውስብስብ እንደነበርና የስዊድን መንግስት እንዲህ አይነት ችግሮች ሲያጋጥሙት ዜጎቹን ለመታደግ እንዴት እንደሚንቀሳቀስ ይተነትናል ተብሏል፡፡
የመፅሃፉ ደራሲ ለመገናኛ ብዙኃን በሰጡት አስተያየት፤በስዊድንና በኢትዮጵያ መንግስት መካከል ከምርጫ 97 በፊት በሁሉም መስክ መረዳዳትና መተባበሮች ነበሩ፣ከምርጫው በኋላ ግን በሰብአዊ መብትና ዴሞክራሲ ጉዳዮች ላይ አብዛኞቹ ምዕራባዊያን ሃገሮች ሲያደርጉት እንደነበረው የስዊድን መንግስትም በጉዳዩ ላይ ወቀሳ በመሰንዘሩ፣የሁለቱ ሃገራት ግንኙነት በመጠኑ ሻክሮ ነበር ብለዋል፡፡ አምባሳደሩ አክለውም በሁለቱ ሃገራት መካከል የነበረው የቀደመ ግንኙነት መልካም መሆኑን ከግምት ውስጥ በማስገባት የጋዜጠኞቹ ጉዳይ በፍጥነት እልባት ያገኛል የሚል ተስፋ የነበራቸው ቢሆንም በተቃራኒው  በአታካችና ውስብስብ ሂደቶች ውስጥ ለማለፍ ተገደዋል ብለዋል፡፡
አምባሳደሩ ጋዜጠኞቹን ለማስፈታት ከመንግስት ባለስልጣናት ጋር ብቻ ሳይሆን እንደ ፕ/ር ኤፍሬም ይስሃቅ ከመሳሰሉት ሰዎች ጋርም ይገናኙ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ “ፕ/ር ኤፍሬም ይስሃቅ የማከብረውና የማደንቀው ሰው ነው፡፡ ጋዜጠኞቹን የማስፈታት ሂደት ቀልጣፋ እንዲሆን ተባብሮናል” ሲሉ በመፅሃፋቸው ገልፀዋል፡፡
ጋዜጠኛ ማርቲን ሲመይ እና ፎቶግራፈር ጆን ፐርሰን በሐምሌ 2003 ዓ.ም በሶማሌ ክልል በኦጋዴን አካባቢ በሽብርተኝነት ከተሰየመው የኡጋዴን ነፃ አውጪ ግንባር ጋር ሲንቀሳቀሱ ከ150 ያህል ታጣቂዎች ጋር በቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን በፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት፣ በህገ-ወጥ መንገድ ወደ ሃገር ለመግባት መሞከርን ጨምሮ የሽብር ቡድን መደገፍና ማበረታታት እንዲሁም ማስተዋወቅ የሚሉ ክሶች ቀርቦባቸው እንደነበር ይታወሳል፡፡ ወራት በፈጀው የፍርድ ሂደትም ሁለቱ ጋዜጠኞች እያንዳንዳቸው በ11 ወራት እስራት እንዲቀጡ የተወሰነ ሲሆን ለዓመት ከሁለት ወር ያህል ከታሰሩ በኋላ በይቅርታ ተለቀው ወደ አገራቸው መሄዳቸው  ይታወቃል፡፡

Published in ዜና

ለውጪ ገበያ የሚቀርበውን የጥጥ ክር ምርት በእጥፍ ያሳድጋል
ኢትዮጵያን በአለም ከታወቁት ጥቂት የጥጥ ክር አምራች አገራት አንዷ ለማድረግ ያቀደው ኤስቪፒ ቴክስታይልስ በኮምቦልቻ በ11 ቢሊዮን ብር ወጪ ዘመናዊ የጥጥ ክር ፋብሪካ ሊገነባ መሆኑን አስታወቀ፡፡
በኮምቦልቻ የሚገነባው ፋብሪካው  በቀን እስከ 272.9 ቶን የሚደርስ ምርጥ የጥጥ ክር የማምረት አቅም እንዳለው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ፋብሪካው ምርት ሲጀምር፣ አገሪቱ በአሁኑ ጊዜ ለውጭ ገበያ የምታቀርበውን ጥራቱን የጠበቀ የጥጥ ክር ምርት፣ በእጥፍ እንደሚያሳድገው የተገለፀ ሲሆን የአገሪቱን የልማት እቅድ መሰረት አድርጎ የተቀረጸው ፕሮጀክቱ፣ በአሁኑ ጊዜ ከቅድመ ዝግጅት ደረጃ አልፎ ወደ ትግበራ እንቅስቃሴ ለመሸጋገር እያኮበኮበ ነው ተብሏል፡፡
የፋብሪካው መገንባት በውጭ ንግዱ ዘርፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክት ሲሆን ለበርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች የስራ ዕድል እንደሚፈጥርና  የተለያዩ ጥቅሞችን እንደሚያስገኝ ተነግሯል፡፡
እ.ኤ.አ በ1898 ዓ.ም  የተመሰረተውና የፕሮጀክቱ ባለቤት የሆነው የህንዱ ፒቲ ግሩፕ፣ በስሩ በርካታ ኩባንያዎችን የሚያስተዳድር ሲሆን  በጨርቃ ጨርቅ፣ በፋይናንስ፣ በሸቀጣሸቀጥ፣ በሪል እስቴትና በጌጣጌጦች የንግድ  ስራዎች ላይ በመሰማራት ትርፋማ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል ተብሏል፡፡

Published in ዜና
Page 4 of 13