በአባይ ወንዝ ላይ እየተገነባ ያለውን የታላቁን ህዳሴ ግድብ በመቃወም ግንባታውን ለማደናቀፍ የተለያዩ ዘመቻዎችን እያካሄደች ያለችው ግብፅ፤ ግድቡ ሁለቱን ሃገራት የጋራ የሚጠቅም ከሆነ ቦንድ በመግዛት በገንዘብ ለመደገፍ እንደምትፈልግ የሃገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማስታወቃቸውን የዜና ምንጮች ገለፁ፡፡
በቤልጅየም ብራሰልስ እየተካሄደ ባለው የአፍረካ ህብረት እና የአውሮፓ ህብረት የጋራ ጉባኤ ላይ ለመካፈል የተጓዙት የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ነቢል ፋህሚ  የህዳሴ ግድብን ለማስቆም ከፍተኛ ዘመቻ ሲያካሂዱ ሰንብተዋል፡፡ ሮያል ኢንስቲትዪት ፎር ኢንተርናሽናል ሪሌሽን በተባለው ተቋም ሃሙስ እለት ባደረጉት ንግግርንና፣ ሃገራቸው የህዳሴውን ግድብ ግንባታ በገንዘብ ለመደገፍ ማቀዷን አስታውቀው ግድቡ ተሰርቶ ሲጠናቀቅ ግድቡን የማስተዳደር ስልጠን ከሁለቱ ሃገራት በተውጣጣ ኮሚቴ ስር መሆን አለበት፡፡
ቀደም ሲል የህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያና የግብፅ የጋር ፕሮጀክትነት እንዲሆን ተመሳሳይ ጥያቄ መቅረቡ የሚታወስ ሲሆን፤ በኢትዮጵያ መንግስት ግን ጉዳዩ ከሉአላዊነት ጋር የተያያዘ መሆኑን በማመልከት ጥያቄውን ውድቅ አድርጎታል፡፡  ግድቡን የጋራ ለማድረግ በሚሆንበት ጉዳይ ላይ አበክራ እንደምትሰራ የተናገሩት ነቢል ፋህሚ፤ ከግድቡ ጋር በተያያዘ የግብፅን ጥቅም የሚቀናቀን ጉዳይ ላይ ግን ትዕግስት እንደሌላት ተናግረዋል፡፡ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በጉባኤው ላይ ከአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ኃላፊ ካትሪን ጋር የመከሩ ሲሆን በጉባኤው ላይም የግድቡ ጉዳይ መነጋገሪያ እንደሆነ ኃላፊዋን መጠየቃቸው ተጠቁሟል፡፡ የህዳሴው ግድብ የመሰረት ድንጋይ የተጣለበት 3ኛ አመት መከበሩን በተመለከተ የግብፅ የሚዲያ ተቋማት በርካታ ዘገባዎች ሲያቀርቡ የሰነበቱ ሲሆን፤ የተለያየ አቋም አስተጋብተዋል፡፡ ግድቡ ሁለቱንም ሃገራት እንደሚጠቅም መሆኑ የሚገልፅ ዘገባ ያሰራጩ የሚዲያ ተቋማት እንዳሉዋሉ፤ ሌሎች ደግሞ ግብፅ ጥቅሟን ለማስከበር በተለይም በ1902 እ.ኤ.አ ሚኒልክ ፈርመውበታል የተባለውን ስምምነት በመጥቀስ በአለማቀፉ ፍ/ቤት ክስ እንድታቀርብ እየመከሩ ነው፡፡
የግብፅ ምሁራንና ባለስልጣናት በተደጋጋሚ የግድቡ መገንባት ማንኛውም 95 በመቶ ውሃ ፍላጎቷን ከናይል በምታገኘው ሃገራቸው ላይ የውሃ መጠኑን በ20 በመቶ በመቀነስ ጉዳት ያመያል ሲሉ እየተከራከሩ ሲሆን አንዳንድ የኢንጅነሪንግ እውቀት ያላቸው ምሁራኖቿ ግን ከዚህ በተቃራኒው ግድቡ ዓመቱን ሙሉ የውሃ ፍሰት ሳይቀንስ እንዲዘልቅ ይረዳል ሲሉ መከራከሪያ ሲያቀርቡ ተደምጧል፡፡
ግንባታው ከተጀመረ 3 ዓመት የሆነው የታላቁ ህዳሴ ግድብ 32 በመቶ ስራው የተጠናቀቀ ሲሆን ለግድቡ ግንባታ 11.5 ቢሊዮን ብር ከህብረተሰቡ ቃል የተገባ ሲሆን አጠቃላይ ወጪው 80 ቢሊዮን ብር እንደሆነ ተመልክቷል፡፡  

Published in ዜና

   ሰሞኑን በቤልጂየም መዲና ብራሰልስ በተካሄደው የአፍሪካ አውሮፓ ጉባኤ ላይ የተገኙት የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ነቢል ፋሃሚ፤ ከጉባኤው ጎን ለጎን  ታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ላይ ጫና ለማሳደር፣ ከመንግስታቱ ድርጅት ዋና ፀሀፊ ባን ኪ ሙንና ከአውሮፓ የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ካትሪን አሽተን ጋር ተወያዩ፡፡
የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፤ በብራሰልስ  የባን ኪ ሙን መኖሪያ ቤት ተገኝተው በታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ዙሪያ የተወያዩ ሲሆን ግብፅ በኢትዮጵያ ላይ ጫና ለማሳደር የጀመረችው ዓለም አቀፍ እንቅስቃሴ አካል ነው ተብሏል፡፡ ጉባኤው ከመጀመሩ አንድ ቀን ቀደም ብሎም ሚኒስትሩ ከአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ካትሪን አሽተን ጋር ተመሳሳይ ውይይት ማድረጋቸው ታውቋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ነቢል ፋሂም፤ እዚያው ብራሰልስ ካገኟቸው የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ቴዎድሮስ አድሀኖም ጋርም ተወያይተዋል፡፡ የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ባለፈው ሰኞ ባወጣው መግለጫ፤“የግብፅን የውሀ ደህንነት ለማስጠበቅ የተቀናጀ የድርጊት መርሀ ግብር ተነድፏል፣ ጉዳዩም ደረጃ በደረጃ እየተሄደበት ይገኛል፣ ይህን የሚያስፈፅም ልዩ የህግ ኮሚቴ ተቋቁሟል፡፡ ግብፅ በአባይ ጉዳይ አዲስ ፋይል አታወጣም፡፡  አባይ የብሔራዊ ደህንነት ጉዳይ ስለሆነ ፖለቲካዊ፣ ህጋዊና  የቴክኒክ ጉዳዮችን ያካተተ መርሀ ግብር ተነድፏል” ብሏል፡፡
በሌላ በኩል በግብፅ የኢትዮጵያ አምባሳደር መሀሙድ ድሪር በአደራዳሪዎች ዙሪያ ሰሞኑን በሰጡት አስተያየት፤ “ግብፅ እና ኢትዮጵያ በግድቡ ዙሪያ ከራሳቸው ውጪ አደራዳሪ አይፈልጉም” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

        ቦታው ለልማት ይፈለጋል ተብሎ ቤት ሲፈርስ፣መጠለያ አጥተው ቤተ-መንግስት ስር መኖር የጀመሩት  48 ቤት አልባዎች፤ሰሞኑን “በጅብ መንጋ ልንበላ ነው” ሲሉ ምሬትና አቤቱታቸውን ገለፁ፡፡ ከጅቦቹ ይከላከሉናል ብለን የሰበሰብናቸው ውሾችም በወረዳው ባለስልጣናት በመርዝ ስለተገደሉብን ከፍተኛ ስጋት ላይ ነን ብለዋል - ቅሬታ አቅራቢዎቹ።
 የወረዳ ስምንት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ደሳለኝ ደበሌ ስለጉዳዩ ጠይቀናቸው ሲመልሱ፤በወረዳው ሸራተንና ፓርላማ በመባል የሚታወቁ ሁለት ፕሮጀክቶች እንዳሉ ገልፀው፤ በሸራተን ፕሮጀክት ለመልሶ ማልማት 1319 ቤቶች ሲፈርሱ፣ምትክና ካሳ እየሰጠን መመሪያው የሚፈቅድላቸውን አስተናግደናል ብለዋል፡፡ በወረዳው ረጅም ዓመት ለኖሩ ምንም መረጃ የሌላቸው ከ60 በላይ ሰዎችም አስተናግደናል ይላሉ- ሥራ አስፈፃሚው፡፡ በሸራተን ዙሪያ በጥገኝነትና በተከራይነት ከ15-23 ዓመት እንደኖሩና የቀበሌ መታወቂያ እንዳላቸው የነገሩን  ቤት አልባዎች የወረዳ ኃላፊዎቹን ይወቅሳሉ፡፡ “ከዛሬ ነገ ቤት ይሰራላችኋል፤መጠለያ ተፈልጎ ትገባላችሁ” ሲሉን ቢቆዩም እስካሁም መፍትሄ አላገኘንም ይላሉ፡፡ አሁን ከቤቱም በላይ ሃሳብ የሆነባቸው የጅቦቹ ጉዳይ ነው፡፡ ጅቦች ከነጋ በኋላም እየመጡብን ከፍተኛ ስጋት ፈጥረውብናል ብለዋል - ነዋሪዎቹ፡፡
“ወረዳው ቀደም ሲል በእኛው ጉዳይ ከአዲስ አድማስ ጥያቄ ቀርቦለት ‘ከክፍለ ከተማው ጋር ተመካክረን የመጠለያ ቦታ አፈላልገን አግኝተናል’ የሚል ምላሽ ቢሰጥም እኛ ግን እስካሁን መፍትሄ አላገኘንም” ያሉት ስማቸውን መግለፅ ያልፈለጉ የአምስት ልጆች አባት፤ በላስቲክ ቤት ውስጥ መኖራቸውን በመቀጠላቸው  ጅቦች ስጋት እንደፈጠሩባቸው ጠቁመው፣ “ዜጎች እንደመሆናችን መንግስት መፍትሄ ይፈልግልን” ሲሉ ተማፅነዋል፡፡
የወረዳ ስምንት ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ደሳለኝ በበኩላቸው፣ “ከዚህ በፊት ጉዳዩን እየተመለከትን በወረዳው እንደመኖራቸው መንግስት የእነዚህን ዜጎች ችግር የመፍታት አቅም ይኖረዋል አይኖረውም የሚለውን ለክ/ከተማው አቅርበናል” ካሉ በኋላ በክፍለ ከተማው ወረዳ 14 ባለወልድ ጀርባ የቆርቆሮ መጠለያ እንደነበረና መጠለያው ከተቃጠለ በኋላ ቦታው ባዶ መሆኑን በማስረዳት፣ እዚያ ቦታ ላይ የቆርቆሮ መጠለያ እንዲሰራ አመልክተን ነበር ይላሉ፡፡  “በወቅቱ የነበሩት የክ/ከተማው ዋና ስራ አስፈፃሚ፣ ከካቢኔ አባላት ጋር ተመካክረው ምን ያህል በጀት እንደሚፈጅ ሰርተን እንድናቀርብ ገልፀው ነበር” ያሉት ስራ አስፈፃሚው፣ በዚህ መሰረት የወረዳው ኮንስትራክሽንና ቤቶች ልማት ባለሙያዎች ምን ምን እንደሚያስፈልግ ሰርተው፣ ለክ/ከተማው አቅርበው ነበር ይላሉ፡፡ ይሁን እንጂ በ2005 ዓ.ም በተካሄደው ምርጫ የመዋቅር ለውጥ በመደረጉና የቀድሞው የክ/ከተማው ስራ አስፈፃሚ ከቦታው በመነሳታቸው፣ የእነዚህ ዜጎች ጉዳይ ሊቀጥል እንዳልቻለ አቶ ደሳለኝ አስረድተዋል፡፡
“በሸራተን ፕሮጀክት ውስጥ ቤት የሚጠይቁት ቤት የማግኘት መብት ኖሯቸው ሳይሆን በወረዳው ብዙ ጊዜ ስለቆዩ የሚቻል ነገር ካለ ብለን የጀመርነው ነበር” ያሉት ዋና ስራ አስፈፃሚው፣ ነገር ግን ገና ለገና ቤት እናገኛለን በሚል ከጎዳና ላይ እየገቡ ላስቲክ ቤት እየሰሩ እንደሚቀመጡና ረጅም አመት የኖሩትን ለመለየት በተደረገው ማጣሪያ 31 አባወራዎች መኖራቸውን፣እነዚህንም ከነቤተሰቦቻቸው በፎቶ አስደግፈው መያዛቸውን ተናግረዋል፡፡ የጅቦቹን ጉዳይ በተመለከተ፣ ኮተቤና በአካባቢው ለመንገድ ስራ ጫካ ሲነካ እየሸሹ የሚመጡ መሆኑን ገልፀው፣ በሸራተን ፕሮጀክት ብቻ ሳይሆን በባለወልድ አካባቢ ለነዋሪዎች ስጋት በመሆናቸው ወረዳው ከደንና የዱር እንስሳት ልማትና ጥበቃ ጋር በመመካከር፣መፍትሄ በመፈለግ ላይ እንደሆኑ ሥራ አስፈፃሚው ተናግረዋል፡፡
“ወደፊት በወረዳው ኮንዶሚኒየም ቤት ደርሷቸው የሚለቀቁ ቤቶች ሲኖሩ ቅድሚያ ይሰጣቸዋል” ያሉት ስራ አስፈፃሚው፤ በዚህ ጊዜ እንዲህ እናደርግላቸዋለን ለማለት እንደሚቸገሩና ለክ/ከተማው ሲወስን ጉዳያቸው እንደሚታይ ተናገረዋል፡፡
ሐምሌ 27 ቀን 2005 ዓ.ም ለንባብ በበቃው አዲስ አድማስ ጋዜጣ “ትራሳቸውን ቤተ-መንግስት ግርጌያቸውን ሸራተን ያደረጉ ቤት አልባዎች” በሚል ርዕስ ስለእነዚሁ 48 ቤት አልባ አባወራዎች መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን በወቅቱ የወረዳ ስምንት ዋና ስራ አስፈፃሚ ከክ/ከተማው ጋር በመነጋገር፤ ለቤት አልባዎች የቆርቆሮ መጠለያ ለመስራት ቦታ በመፈለግ ላይ እንደሆኑ ገልፀውልን ነበር፡፡

Published in ዜና

         የራሺያ የጦር ሃይል የዩክሬንን ድንበር ሰብሮ፣ ክረሚያ የመግባቱን ሰበር ዜና ድፍን ዓለሙ የሰማው በድንጋጤና በመገረም ነበር፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ግን የራሺያ ድርጊት ምንም አይነት አስደንጋጭም ሆነ አስገራሚ ነገር አልነበረውም፡፡ የራሺያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን በዩክሬን ላይ የፈፀሙትን አይነት ድርጊት ምቹ ጊዜና አጋጣሚ ካገኙ ከመፈፀም እንደማይመለሱ ያዘጋጁትን እቅድ እንደ ሀገር ምስጢር ጨርሶ ደብቀውት አያውቁም፡፡
ከዛሬ አስራ አምስት በፊት ነሐሴ 16 ቀን 1999 ዓ.ም በፕሬዚዳንት ቦሪስ የልሲን የራሺያ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው የተሾሙት ቭላድሚር ፑቲን፤ አዲሱን ሹመታቸውን ባፀደቀላቸው የራሺያ ዱማ (ፓርላማ) ፊት ቀርበው ንግግር አድርገው ነበር፡፡ ያኔ ያደረጉት ንግግር ለወጉ ያህል የሚደረግ ተራ ንግግር ሳይሆን በስልጣን ዘመናቸው ሊያከናውኑት የሚፈልጉትን ዝርዝር የስራ እቅዳቸውን የሚጠቁም ነበር፡፡
ቭላድሚር ፑቲን ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው በተሾሙበት ወቅት ራሺያ ውቃቤ ርቋት ነበር፡፡ መቸም ቢሆን ለማንም በምንም አይረታም እየተባለ ይነገርለት የነበረው የራሺያ ጦር፣ ጠቅላላ ህዝቧ ራሺያ ካሰማራችው የጦር ሃይል ብዛት በእጅጉ በሚያንሰው በቺቺኒያ በአሳፋሪ ሁኔታ ተሸንፎ ነበር።
ቀደም ባለው ጊዜ የራሺያ ዋነኛ አጋርና የዋርሶ ጦር ቃል ኪዳን ድርጅት አባላት የነበሩ ሶስት የምስራቅ አውሮፓ ሀገራት፣ የኔቶ አባል ሀገር በመሆናቸው የምዕራቡን አለም ህብረት ክልል አፍንጫዋ ስር አድርሰውት ነበር፡፡ ራሺያን ከፍ ያለ ችግር ውስጥ የከተታትን ይህን ምስቅልቅል በቁርጠኝነት በመታገል እልባት ያበጁለታል ተብለው በከፍተኛ ተስፋ የተጠበቁት ፕሬዚዳንት ቦሪስ የልሲንም የመሪነት ነገር አለሙን ሁሉ እርግፍ አድርገው ትተው፣ ገና ሰማይና መሬት በቅጡ ሳይላቀቅ፣ ቮድካ በመጨለጥ ጥንብዝ ብሎ መስከርን ስራዬ ብለው የያዙበት፣ በዚህም የተነሳ ጤናቸው ክፉኛ ተቃውሶ ጐምላላው ሞት ከዛሬ ነገ ወሰድኳቸው እያለ የሚያስፈራራበት ወቅት ነበር፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ፑቲን ግን ለዚህ ሁሉ ውጥንቅጥ ችግር መፍትሔ ይሆናል ያሉትን መላ አበጅተው በልቦናቸው ይዘው ነበር፡፡ እናም የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ስልጣናቸውን በሙሉ ድምጽ ባፀደቀላቸው የራሺያ ዱማ ፊት ቀርበው ባደረጉት ንግግር እንዲህ አሉ፤ “መንግስት መስራት ያለበትን ስራዎች ሁሉ በዚህ ንግግሬ ዘርዝሬ አልጨርሰውም፡፡ የሆኖ ሆኖ አንድ ነገር ግን በእርግጠኝነት አውቃለሁ፡፡ ከላይ ወደታች ያለው የእዝ ሰንሰለት ሳይጠናከር፣ በመላው ራሺያ መሰረታዊ ስርአት ሰፍኖ ጥብቅ የሆነ ስነምግባር ሳይጠበቅ፣ አንዱ ስራ እንኳ ይሰራል ማለት ዘበት ነው፡፡”
ጠቅላይ ሚኒስትር ፑቲን የሀገራቸውን የራሺያን ነገር ሲያስቡ በእጅጉ የሚቆጩበት ሌላም ጉዳይ ነበራቸው፡፡ ቭላድሚር ፑቲን የሶቪየት ህብረት ዝናና ተፈሪነት ሰማይ በነካበት ዘመን የተወለዱ የሶቪየት ህብረት ወርቃማው ዘመን ልጅ ናቸው። ያኔ እሳቸው በተወለዱበት በ1952 ዓ.ም ሶቪየት ህብረት በሁለተኛው የአለም ጦርነት ወቅት የናዚ ጀርመንን ጦር ሃይል እንዴት እንዳሸነፈች ዝናዋ አለመጠን ገዝፎ የሚተረክበት ጊዜ ነበር፡፡
ያ ወቅት ሶቪየት ህብረት ስፑትኒክ የተባለችውን መንኮራኩሯን ወደ ጠፈር ያመጠቀችበት፣ ሃይድሮጅን ቦንብን መስራት የቻለችበት፣ ዩሪ ጋጋሪን የተባለውን ጠፈርተኛዋን ወደ ጠፈር በመላክ በዓለም ቀዳሚ የሆነችበት፣ ላይካ የተባለውን ውሻም ወደ ጠፈር በመላክ ከአለም አንደኛ የተባለችበት ወርቃማ የዝናና የክብር ጊዜ ነበር፡፡
በቀጣዮቹ አመታትም በ1956 ዓ.ም በሀንጋሪ፣ በ1968 ዓ.ም ደግሞ በቼኮዝሎቫኪያ የተቀሰቀሰውን “ፀረ - አብዮት” አመጽ፣ ዝነኛውን ቀዩን ጦሯን አለአንዳች ማወላወል አዝምታ ሰጥ ረጭ በማድረግ፣ ባለብረት ክንድ ሀገር መሆኗን ያስመሠከረችበት ወቅት ነበር፡፡
ቭላድሚር ፑቲን ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው በተሾሙበት ወቅት የነበረችው ሀገራቸው ግን በዓለም አቀፉ መድረክ የነበራት ቦታ ከድሮ ዝናና ክብሯ በእጅጉ የራቀ፣ እዚህ ግባ የማይባል ዝቅተኛ ቦታ ነበር፡፡ እንደእውነቱ ከሆነ፣ በወቅቱ የአለማችን የፖለቲካ መድረክ ራሺያን ከመሪ ተዋንያኖች ተራ አውጥቷት፣ የአለም ህዝብም ረስቷት ነበር፡፡
ለጠቅላይ ሚኒስትር ቭላድሚር ፑቲን እንዲህ ያለው የራሺያ አለማቀፋዊ ሁኔታ መቸም የማይበርድ የእግር እሳት ነበር፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው እስከተሾሙበት ጊዜ ድረስም ይህን ሁኔታ ለመለወጥ የሚችሉበትን “ቅዱስ አጋጣሚና ቀን” ለዘመናት ሲመኙ ኖረዋል፡፡
ልክ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው እንደተሾሙም ያ ሲመኙት የኖሩት ቀን እንደመጣላቸው በልባቸው አመኑ፡፡ እናም አንዳችም ጣጣ ሳያበዙና በዲፕሎማሲያዊ አነጋገር ነገር ሳያወሳስቡ ለዱማው እንዲህ በማለት እቅጩን ተናገሩ፣ “ራሺያ ለአያሌ ዘመናት ገናናና ታላቅ ሀገር ሆና ኖራለች፡፡ ወደፊትም ትኖራለች፡፡ የራሺያ የግዛት አንድነት ጉዳይ ለድርድር የሚቀርብ  አይደለም፡፡ የግዛት አንድነታችንን በሚዳፈር በማንኛውም አካል ላይ ጠንካራ እርምጃ እንወስዳለን፡፡ በቀድሞው የሶቭየት መሬትም ሆነ በሌሎች ቦታዎች ላይ ህጋዊ የሆነ የብሔራዊ ጥቅም ጥያቄ ሁሌም ቢሆን አለን፡፡ በዚህ ረገድ የብሄራዊ ጥቅም ማስጠበቂያ ክንዳችን ለአፍታም ቢሆን መዛል የለበትም፡፡ እኛ የምናቀርበው ጥያቄም ሆነ አስተያየት በሌሎች ዘንድ ተንቆ ችላ እንዲባል መቸም ቢሆን መፍቀድ የለብንም፡፡”
ይህ ንግግር ቭላድሚር ፑቲን የራሺያን የውስጥና የውጪ ችግሮች ያስወግዳል ብለው አምነውበት ያወጡት እቅድ ዝርዝር መግለጫ ነው፡፡ ይህንን ንግግራቸውን ያደረጉትም በምስጢርና ለቁልፍ የስራ ባልደረቦቻቸው ብቻ አልነበረም፡፡ ይልቁንም ለመላው ዓለምም ጭምር እንጂ፡፡
ይህ የፑቲን እቅድ በእጅጉ የተስማማት የመሰለችው የራሺያ የስልጣን አድባርም ከፍ ባለ ልግስና ፊቷን አዙራላቸዋለች፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትርነት ወደ ፕሬዚዳንትነት ስታሸጋግራቸው የመንፈቅ ጊዜ እንኳ አልፈጀባትም፡፡ ከ2008 እስከ 2012 ዓ.ም በፕሬዚዳንት ዲሚትሪ ሜድቬዴቭ የስልጣን ዘመን ለሁለተኛ ጊዜ በጠቅላይ ሚኒስትርነት ከማገልገላቸው በቀር እነሆ ዛሬም ድረስ የፕሬዚዳንትነት ስልጣኑን ባርካላቸዋለች፡፡
ቭላድሚር ፑቲን በንግግራቸው በግልጽ እንዳስቀመጡት፤ የሀገር ውስጥ ፖሊሲያቸው በምድረ ራሺያ መረጋጋትን ማስፈንና ጠንካራ ከላይ ወደታች የሚፈስ የእዝ ተዋረድን ማረጋገጥ ላይ ሲያተኩር፣ የውጭ ፖሊሲያቸው ደግሞ በዋናነት ራሺያን ወደ ቀድሞ ገናና ዝናና ክብሯ በመመለስ፣ በዓለም አቀፍ የፖለቲካ መድረክ መሪ ተዋናይነት ዳግመኛ መመለስን ዋነኛ ግቡ ያደረገ ነው፡፡
መላው ዓለም ያኔ እንዲያ በግልጽና በዝርዝር የወደፊት እቅዳቸውን ያቀረቡበትን ንግግር በጥሞና አዳምጧቸውና አስታውሶት ቢሆን ኖሮ፣ ዛሬ ጦራቸውን ወደ ዩክሬን ሲያዘምቱ አይቶና ሰምቶ ክፉኛ ባልደነገጠ ነበር፡፡
ቭላድሚር ፑቲን ግን የስልጣን ዘመናቸውን አሀዱ ብለው ከጀመሩበት በነሐሴ 16 ቀን 1999 ዓ.ም ጀምሮ፣ ከመስከረም 11 ቀን 2001 ዓ.ም የአሜሪካ የሽብር ጥቃት እስከ አሁኑ የዩክሬን አብዮት ድረስ ከላይ የጠቀስኳቸውን የሀገር ውስጥና የውጭ ፖሊሲያቸውን ለማሳካት፣ ታሪክ የፈጠረላቸውን አጋጣሚዎች ሁሉ አለአንዳች ማመንታት ለመጠቀም ሞክረዋል፡፡ ስልጣናቸውን ለመቀናቀን ሞክረዋል ከተባሉት የቀድሞው የራሺያ ቁጥር አንድ ከበርቴ ሙሚካኤል ኮዶሮቭስኪ እስከ የቸቺኒያ አማጺያን ድረስ ያሉትን “አፈንጋጮች” እንደ ብረት በጠነከረው ክንዳቸው ልክ በማስገባት የሀገር ውስጥ መረጋጋት ፈጥረዋል፡፡
በዓለም አቀፍ የፖለቲካ መድረክ ላይም ከሁለተኛው ዙር የኢራቅ ወረራ እስከ ሶሪያ ህዝባዊ አመፅ ድረስ በተካሄዱት አለምአቀፍ የፖለቲካ መድረኮች፣ ራሺያ ከመሪ ተዋንያኖች አንዱ ሆና መተወን ችላለች፡፡
ይህ ሁሉ ግን የቆፍጣናውና የብሔርተኛውን የፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲንን ልብ ሊሞላው አልቻለም፡፡ የታላቁ አባት ሀገር የሲቪየት ራሺያ ግንባታ በፖለቲካው ብቻ ሳይሆን በግዛትም በደንብ መካሄድ ይኖርበታል፡፡ “በቀድሞው የሶቪየት መሬትም ሆነ በሌሎች ቦታዎች ላይ ህጋዊ የሆነ የብሔራዊ ጥቅም ጥያቄ ሁሌም ቢሆን አለን። በዚህ ረገድ የብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቂያ ክንዳችን ለአፍታም ቢሆን መዛል የለበትም፡፡” ይህን የቭላድሚር ፑቲን ታሪካዊ ንግግር መቼም ቢሆን ልንረሳው አይገባም፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ የአሜሪካንና የአውሮፓ ህብረትን ዛቻና ማዕቀብ ከምንም ሳይቆጥሩ የዩክሬን አካል የነበረችውና ትውልደ ራሺያውያን የሚበዙባት የክረሚያ ግዛት፣ የታላቁ አባት ሀገር ሶቪየት ራሺያ አባል እንድትሆን ያደረጉት ለምን እንደሆነ በወጉ ልንረዳው የምንችለው ይህን ንግግራቸውን በሚገባ ማስታወስ ከቻልን ብቻ ነው፡፡
እንግዲህ ግራም ነፈሰ ቀኝ፣ ፕሬዚዳንት ፑቲን በዩክሬንና በክሚያ ላይ የፈፀሙት ድርጊት፤ ከዚህ በፊት የአፍሪካ ችግር ብቻ ተደርጎ ይቆጠር የነበረው በተለያዩ ሀገራት ተከፋፍለው የሚኖሩ አንድ አይነት ህዝቦች፣ በአንድ ሀገር ውስጥ ተጠቃለው ለመኖር የሚያደርጉት ትግል፣ (irridentism) አዲሱ የአለማችን የ21ኛው ክፍለ ዘመን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግር ሆኖ በዓለም አቀፍ የፖለቲካ መድረክ ላይ ብቅ እንዲል አድርገውታል፡፡
ይህ ጉዳይ ደግሞ በተለይ በባልቲክ ሀገራት ዘንድ ከፍተኛ ጭንቀትን ፈጥሯል፡፡ ይህ ደግሞ አለምክንያት አይደለም፡፡ ለምሳሌ ላቲቪያና ሊቱዋኒያ ከጠቅላላው በጠቀወላላው ህዝባቸው 30 በመቶ የሚሆኑት ትውልደ ራሺያውን ሲሆኑ በኢስቷኒያ ደግሞ ቁጥራቸው 25 በመቶ ይሆናል። አሁን ትልቁ ጥያቄ የፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ቀጣይ እርምጃና የእነዚህ አገሮች እጣ ፈንታ ምን ይሆናል የሚለው ነው፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ
Monday, 07 April 2014 15:21

ፑቲንን በአጭሩ

ፕሬዚደንት ቭላድሚር ቭላድሚሮቪች ፑቲን፤ የፋብሪካ ሠራተኛ ከነበሩት እናታቸው ማርያ ኢቫኖቫ ፑቲና እና የሶቪየት ህብረት ባህር ሃይል ወታደር ከነበሩት አባታቸው ቭላድሚር ስፒሪዶኖቪች ፑቲን ቀድሞ ሌኒንግራድ በመባል በምትጠራው ቅዱስ ፒተርስበርግ ከተማ እ.ኤ.አ ጥቅምት 7 ቀን 1952 ዓ.ም ተወለዱ፡፡
ከመኖሪያ ቤታቸው አቅራቢያ በሚገኘው የባስኮቭ ትምህርት ቤት የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ፣ ለከፍተኛ ትምህርት ወደ ሌኒንግራድ ዩኒቨርሲቲ አመሩ፡፡ በዚህ ዩኒቨርሲቲ የህግ ትምህርት ቤት፣ የአለም አቀፍ ህግና ኢኮኖሚክስ ትምህርታቸውን ከተከታተሉ በኋላ በ1975 ዓ.ም ተመርቀው ወጡ፡፡
ቭላድሚር ፑቲን፤ አባታቸው ያገለግሉበት በነበረው የሶቪየት ህብረት የባህር ሃይል ውስጥ ኬጂቢ ተብሎ ከመቋቋሙ በፊት ኤንኬቪዲ በሚል ይጠራ በነበረው የሶቪየት ህብረት የደህንነትና የስለላ ድርጅት ውስጥ አባል እንደነበሩ ከልጅነታቸው ጀምሮ በሚገባ ያውቁ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የአባታቸውን ፈለግ በመከተል ሰላይ ለመሆን ምንም አይነት ፍላጐት አልነበራቸውም። ያኔ የነበራቸው ከፍተኛ ፍላጐት የስድስተኛ ክፍል ተማሪ ሳሉ ጀምረውት አለመጠን ፍቅር ባሳደረባቸው የጁዶ ስፖርት በመግፋት፣ በምድረ ሶቪየት ህብረት ከፍተኛ ዝናን መጐናፀፍ ነበር፡፡
የዘጠነኛ ክፍል ተማሪ በነበሩበት ወቅት ግን እንዲህ ሆነ፡፡ የሶቪየት ህብረት የማስታወቂያ ሚኒስቴር የስለላ ታሪክ ያለው ተከታታይ ፊልም ለህዝቡ በቴሌቪዥን ማቅረብ ጀመረ። እንደማንኛውም የሶቪየት ህብረት ዜጋም ወጣቱ ቭላድሚር ፑቲን ይህንን ፊልም ስራዬ ብለው መከታተል ጀመሩ፡፡ ሳያስቡት ግን በወቅቱ በሶቪየት ህብረት ታዋቂ የፊልም ተዋናይ የነበሩት ቪያችስላቭ ቲኮኖቭና ጆርጂ ዚህዞኖቭ ይተውኑት በነበረው የሰላይ ገፀ - ባህርያት በከፍተኛ ፍቅር ወደቁ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮም በፊልም እንዳዩዋቸው ሰላዮች መሆን የቀንም ሆነ የለሊት ህልማቸው ሆነ፡፡
በ1975 ዓ.ም ከሌኒንግራድ ዩኒቨርሲቲ ተመርቀው በወጡ ልክ በሁለተኛ ወራቸውም የሶቪየት ህብረት የስለላ ድርጅት ኬጂቢን በጀማሪ ሰላይነት ተቀላቀሉ፡፡ ቭላድሚር ፑቲን ምርጥ ሰላይ ለመሆን የነበራቸው ከፍተኛ ምኞትና ህልም እንዲሁ መና አልቀረባቸውም። በብዙ የኬጂቢ ሰላዮች ዘንድ እምብዛም ባልታየ ሁኔታ የስለላ ብቃታቸውን ማስመስከር የቻሉት ፑቲን፤ ባጭር ጊዜ ውስጥ ትከሻቸውን ለኮሎኔልነት ማዕረግ አበቁት፡፡ ሰውየው በዚህ ብቻ አላበቁም። በ1986 ዓ.ም በያኔዋ ምስራቅ ጀርመን የኬጂቢ ቢሮ ሃላፊ በመሆን ለመሾም ችለዋል፡፡
በ1990 ዓ.ም የያኔዋ ሶቪየት ህብረት ስትፈራርስ፣ ለ16 አመታት በከፍተኛ ብቃት ያገለገሉበትን ኬጂቢን በጡረታ ተሰናብተው በመውጣት፣ በራሺያ የፖለቲካ መድረክ የእጣ ፈንታቸውን ለመሞከር ጓዛቸውን ቀርቅበው ወደ ትውልድ ከተማቸው ወደ ቅዱስ ፒተርስበርግ አቀኑ፡፡
ቭላድሚር ፑቲን የፖለቲካውን አለም ለመቀላቀል ወስነው፣ በ1990 ዓ.ም ማብቂያ ላይ ወደ ሌኒንግራድ ወይም ቅዱስ ፒተርስበርግ ከተማ ያመሩበት እግራቸው እርጥብ ነበር። እዚያ እንደደረሱ በመጀመሪያ ያገኙት በሌኒንግራድ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ በነበሩበት ወቅት አስተማሪያቸውና ዋና ወዳጃቸው የነበሩትን አናቶሊ ሶብቸክን ነበር፡፡ ሁለቱ በተገናኙበት ወቅት ደግሞ የቀድሞው መምህራቸው ፕሮፌሰር አናቶሊ ሶብቸክ የቅዱስ ፒተርስበርግ ከንቲባ ነበሩ፡፡ ከአራት ቀናት በኋላም ከንቲባ አናቶሊ ሶብቸክ፣ ቭላድሚር ፑቲንን የአለም አቀፍ ጉዳዮች ዋና አማካሪያቸው አድርገው ሾሟቸው፡፡ ከንቲባ አናቶሊ ሶብቸክ በ1996 ዓ.ም በተደረገው የከንቲባነት ምርጫ በድጋሚ ለመመረጥ ያደረጉት ጥረት ሳይሳካ ቀርቶ በመሸነፋቸው ቭላድሚር ፑቲን የአማካሪነት ስራቸውን ለመልቀቅ ተገደው ስራ ፈት ለመሆን በቁ፡፡
ቭላድሚር ፑቲን በስራ ፈትነት ሁለት ወራት ካሳለፉ በኋላ ግን በክሬምሊን ቤተመንግስት የፕሬዚደንታዊ ንብረቶች አስተዳደር መምሪያ ሃላፊ የነበሩት የፓቬል ቦሮዲን ምክትል በመሆን እንዲያገለግሉ ጨርቄን ማቄን ሳይሉ ባስቸኳይ ወደ ሞስኮ እንዲመጡ፣ ፕሬዚደንት ቦሪስ የልሲን ጥሪ አቀረቡላቸው፡፡ መጋቢት 26 ቀን 1997 ዓ.ም ፕሬዚደንት የልሲን፤ ቭላድሚር ፑቲንን ምክትል የቢሮ ሃላፊ አድርገው ሾሟቸው፡፡
በቀጣዩ አመት ሐምሌ 25 ቀን 1998 ዓ.ም ቭላድሚር ፑቲን ከኬጂቢ በኋላ እንደ አዲስ የተቋቋመውና ኤፍኤስ ቢ በመባል የተሰየመው የራሺያ የደህንነትና የስለላ ድርጅት ሃላፊ እንዲሆኑ በፕሬዚደንት ቦሪስ የልሲን ተሾሙ፡፡
በዚህ ሃላፊነት እስከ መጋቢት 29 ቀን 1999 ዓ.ም ድረስ ካገለገሉ በኋላ፣ ነሐሴ 9 ቀን 1999 ዓ.ም እንኳን ሌሎች ራሳቸው ቭላድሚር ፑቲንም ጨርሶ ባላሰቡትና ባልገመቱት ሁኔታ በቮድካ ጨላጭነታቸው የታወቁትና ጤናቸው ከመቸውም ጊዜ በላይ አላወላዳ ያላቸው ፕሬዘደንት ቦሪስ የልሲን፤ የራሺያ ጠቅላይ ሚኒስትር አድርገው ሾሟቸው፡፡ ቭላድሚር ፑቲን ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው በተሾሙ አምስት ወር እንኳ ሳይሞላቸው ታህሳስ 27 ቀን 1999 ዓ.ም ድንገት ስልጣናቸውን የለቀቁትን ፕሬዚዳንት ቦሪስ የልሲን በመተካት የራሺያ ጊዜአዊ ፕሬዚደንት ለመሆን ቻሉ፡፡ የፕሬዚዳንትነት ስራቸውን አሀዱ ብለው የቀደሱትም በዚሁ እለት የቀረበላቸውንና ፕሬዚደንት ቦሪስ የልሲን ከነቤተሰባቸው በምንም አይነት የወንጀል ክስ እንዳይጠየቁ የሚደነግገውን ፕሬዚዳንታዊ አዋጅ በፊርማቸው በማጽደቅ ነበር፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

ለመፍትሄ ያስቸገሩ ሦስት ቀውሶችና በእንጥልጥል የቀሩ ሦስት ምኞቶች
         ሰሞኑን ሲሰራጩ ከነበሩት ዜናዎች መካከል ኬንያንና ሶማሊያን፣ ሱዳንና ኢትዮጵያን የሚመለከቱ አራት የዜና ርዕሶችን ልጥቀስላችሁ። ሰላም ርቋት ከ20 አመታት በላይ በእግሯ መቆም የተሳናት ሶማሊያ ውስጥ፣ ከተለያዩ የአፍሪካ አገራት የተውጣጡ ከ20ሺ በላይ “ሰላም አስከባሪ” ወታደሮች ምን እየሰሩ ነው? ሰላም እያስከበሩ አይደሉም። ሰላም የለማ። ይልቅስ፣ በሃይማኖት አክራሪነቱ ከሚታወቀው አልሸባብ ጋር እየተዋጉ ነው። በርካታ የገጠር ከተሞችን ከአልሸባብ እያስለቀቁ መሆናቸውም ከሰሞኑ ተነግሯል።
በሌላ በኩል በዚሁ ሳምንት ሰኞ እለት፣ ኬንያ ናይሮቢ ውስጥ አሸባሪዎች በፈፀሙት ሁለት የፍንዳታ ጥቃት፣ ስድስት ሰዎች ሞተው ከሃያ በላይ ቆስለዋል። ጥቃቱ የአልሸባብ ሴራ መሆኑን የተናገሩት የኬንያ ባለስልጣናት፣ የሃይማኖት አክራሪነትን የሚያስፋፉ የአልሸባብ ደጋፊዎችን እያደኑ ለመያዝ ዘመቻ መጀመራቸውን ገልፀዋል። ቤት ለቤትና በየጎዳናው አሰሳ እንዲያካሂዱ የታዘዙ ፖሊሶች በአንድ ቀን ውስጥ ከ650 የሚበልጡ ሰዎችን ይዘው አስረዋል። በእርግጥ የአክራሪነትና የሽብር ወሬ የምንሰማው ከኬንያና ከሶማሊያ ብቻ አይደለም። እዚሁ አዲስ አበባ በሽብር የተከሰሱ ሰዎች የፍርድ ሂደት ሲዘገብ ሰንብቶ የለ?
እስከ ፍንዳታና ግድያ ድረስ ባይሄድም፤ አሜሪካ ውስጥ የክርስትና አክራሪዎች እንደ “ኤቮሊሽን” የመሳሰሉ የሳይንስ ትምህርቶችን ለመበረዝ የሚያካሂዱት ዘመቻ ቀላል አይደለም። ግን የባሰ ሞልቷል። ዘመናዊውን ትምህርት በመቃወም “ቦኮ ሃራም” በሚል ስያሜ በናይጄሪያ የግድያ ዘመቻ ሲያካሂድ የከረመውን ድርጅት ማየት ትችላላችሁ። በአንደኛው ሳምንት፣ አዳሪ ትምህርት ቤት ውስጥ ገብቶ 60 ታዳጊ ተማሪዎችን ይፈጃል፤ በሌላ ሳምንት የመኖሪያ ሰፈሮችን በመውረር መንደርተኛውን ይረሽናል። መረጋጋት ያቃታቸው ሊቢያና ቱኒዚያን የመሳሰሉ አገራት ውስጥም፤ አንዱ የሰላም ችግር የሃይማኖት አክራሪነትና ሽብር ነው። የከተማ ሰፈሮችንና የገጠር መንደሮችን ሸንሽነው የተከፋፈሉ አብዛኞቹ የሊቢያ ታጣቂ ቡድኖች፣ አንድም በጎሳ የተቧደኑ አልያም በሃይማኖት አክራሪነት የተደራጁ ናቸው።  የግብፁ ቀውስማ፣ የእለት ተእለት ዜና ነው። ከሰሞኑ በአሸባሪዎች በተፈፀሙት የፍንዳታ ጥቃቶች ከሞቱት ግብፃውያን መካከል አንዱ፣ የጦር ጄነራል ናቸው። የማሊ ጉዳይም ስንዝር አልተሻሻለም። በአንድ ወገን በጎሳ የተቧደኑ ታጣቂዎች፣ በሌላ በኩል ደግሞ አልቃይዳን በአርአያነት የሚከተሉ አክራሪ አሸባሪዎች አሰፍስፈውባታል። ያ አልበቃ ብሎ፤ የሴንትራል አፍሪካ ግጭትና እልቂት ተጨምሮበታል። በሃይማኖት ተቧድነው ለመጨፋጨፍ የተፋጠጡ አክራሪዎች አገሪቱን ደም ለማልበስ የቆረጡ ይመስላሉ።
ለነገሩ፤ በአፍሪካ ብቻ ሳይሆን በሌላውም አለም፤ የሃይማኖት አክራሪነትና ሽብር ያልነካካው አገር ፈልጎ ማግኘት ይከብዳል። የሶሪያና የኢራቅ፣ የፓኪስታንና የአፍጋኒስታንን ብቻ ማለቴ አይደለም። በሃይማኖት አክራሪነት ላይ የተመሰረተው የሳውዲ አረቢያና የኢራን አምባገነንነት ብቻም አይደለም። የሃይማኖት አክራሪነት ከእነዚህም አልፎ፣ ቱርክንና ኢንዶኔዢያን ጭምር ማበላሸት ጀምሯል። ምዕራብ አውሮፓም አልዳነም። ሌላው ቀርቶ፤ የሁስኒ ሙባረክን አምባገነንነት ሸሽተው በእንግሊዝ የተጠለሉ የሙስሊም ብራዘርሁድ አባላት፤ ያስጠለለቻቸውን አገር በአክራሪነት ለማሸበር ከማሴር አልተመለሱም። ለዚህም ነው፤ የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩን፤ የሙስሊም ብራዘርሁድ አባላት ጉዳይ እንደገና እንዲመረመር በቅርቡ ትዕዛዝ ያስተላለፉት። በግልፅ አውጥተን ባንናገረውም፤ በአገራችንም የሃይማኖት ነገር ውስጥ ውስጡን እየተንተከተከ መሆኑን በስሜት ደረጃ ሳናውቀው የምንቀር አይመስለኝም። በአጭሩ፤ ለመፍትሄ ካስቸገሩት የዘመናችን ሦስት ቀውሶች መካከል አንዱ፤ የሃይማኖት አክራሪነት ነው።
በሶማሊያና በኬንያ ዜናዎች የጀመርነውን ርእስ እዚህ ላይ በመግታት ነው ወደ ሱዳን ዜና የምናልፈው። በመጀመሪያም የደቡብ ሱዳንን እንይ። በስልጣን የሚሻኮቱ የደቡብ ሱዳን ገዢ ፓርቲ መሪዎች ባለፈው ታህሳስ ወር፣ የፈጠሩት ግጭት፤ ውሎ ሳያድር በጎሳ ወደ መቧደን እንዳመራ ታስታውሱ ይሆናል። ለጊዜው በአካባቢው አገራት፣ በአሜሪካና በአውሮፓ እንዲሁም በአፍሪካ አንድነትና በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ተደራራቢ ጫና የተነሳ ግጭቱ ቢረግብም፤ በዚያው አልከሰመም። ድርድሩ እየተጓተተ፤ ግጭቱ ቀጥሏል።
በግጭቱ እስካሁን 10ሺ ሰዎች መሞታቸውን በመጥቀስ የተባበሩት መንግስታት ማክሰኞ እለት ባወጣው መግለጫ፤ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰዎች ከመኖሪያቸው ተፈናቅለው ሩብ ሚሊዮን ያህሉ አገራቸውን ጥለው ለመሰደድ እንደተገደዱ አስታውቋል። ብዙዎቹ የተሰደዱት ወደ ኢትዮጵያ ነው። ሌሎች አራት ሚሊዮን ሰዎች ደግሞ፤ ኑሯቸው በግጭት ሳቢያ ተናግቶ ለረሃብ እንደተጋለጡ ዩኤን ገልጿል። እንግዲህ አስቡት። ከጎሳና ከብሄር ተወላጅነት በተጨማሪ ሃይማኖታዊ ገፅታ የነበረው የበርካታ አመታት ጦርነት የተቋጨው ደቡብ ሱዳን ከሰሜን ሱዳን ስትገነጠል ነው። ግን፤ ሰላም አልተገኘም፤ ሃይማኖታዊ ገፅታው ቢደበዝዝም፤ በጎሳ ወይም በብሄር የመቧደን ግጭት አገሪቱን ያመሳቅላት ይዟል።
ምን ያደርጋል? የደቡብ ሱዳን ብቻ አይደለም ችግሩ። ከሃይማኖት አክራሪነት ጋር አያይዤ የጠቃቀስኳቸው ግጭቶች፤ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ፤ በጎሳ ወይም በብሄር የተቧደኑ ግጭቶችንም አዳብለው የያዙ ናቸው። አንድ ቋንቋ የሚነገርባት ሶማሊያ እንኳ፤ ከዚህ ችግር አላመለጠችም። የሃይማኖት አክራሪዎች በሚፈፅሙት ሽብር ብቻ ሳይሆን፣ በጎሳ የተቧደኑ ሰዎች በሚፈጥሩት ግጭትም ነው ሶማሊያ ለ20 አመታት የተበጠበጠችው። ኬንያም እንዲሁ፤ ከጎሰኝነትና ከብሄረተኝነት ጣጣ የራቀች አይደለችም። ፕሬዚዳንቱ ኡሁሩ ኬንያታ፣ ከአገራቸው ውጭ ብዙም ዝር ለማለት ያልቻሉት ወደው አይደለም። ከ7 አመት በፊት ከምርጫ ግርግር ጋር ተያይዞ በተከሰተው ግጭት ላይ፤ ሰዎችን በጎሳ አቧድነው ግድያና ጥቃት እንዲፈፀም አድርገዋል በሚል ክስ፣ ዘሄግ የሚገኘው አለማቀፍ የወንጀል ፍርድ ቤት የመያዣ ትዕዛዝ ቆርጦባቸዋል።
እንዲያው የጎረቤቶቻችንን ጠቀስኩ እንጂ፤ ከብሩንዲ እስከ ናይጄሪያ፣ ከደቡብ አፍሪካ እስከ ኮንጎ፣ ከኢትዮጵያ እስከ ማዳጋስካር፤ የመጠን ልዩነት ይኖራል እንጂ በጎሰኝነት አደጋ ያልተከበበ የአፍሪካ አገር ከወዴት ይገኛል? ግን የአፍሪካ ብቻ ችግር አይደለም። መጤ እና ተወላጅ የሚል መቧደኛ ሰበብ በያዙ ሰዎች አማካኝነት የሚበጠበጡ የደቡብ አሜሪካ አገራት በርካታ ናቸው።
ከጦርነትና ከቀውስ የማይላቀቀው የመካከለኛው ምስራቅንማ ብንተወው ይሻላል። ኢራን እና ሳውዲ አረቢያ፤ ከማንም በላይ እርስ በርስ እንደ ደመኛ ጠላት የሚተያዩት፤ “የሱኒ ሙስሊም” እና “የሺአ ሙስሊም” በሚለው የሃይማኖት አክራሪነት ምክንያት ብቻ አይደለም። “አረብ” እና “ፐርሺያ” በሚል የተወላጅነት ሰበብም ጭምር ነው። እንደ አንድ አገር የቆመች የምትመስለው ኢራቅ፤ በአንድ በኩል “የሱኒ ሙስሊም” እና “የሺአ ሙስሊም” በሚሉ እውቅና ያልተሰጣቸው ድንበሮች ለሁለት እየተሰነጠቀች ነው። በሌላ በኩል ደግሞ፤ “የኩርድ ተወላጆች ግዛት” የሚል ስሜት፣ ያለ አዋጅ ለብቻ የተነጠለ ሶስተኛ ክፍል አለ። ሶሪያም በተመሳሳይ ሁኔታ፤ ለሶስት እየተከፈለች ነው።
ብቻ ምን አለፋችሁ? ዩጎዝላቪያ፣ በሃይማኖትና በጎሰኝነት ብትንትኗ እንደወጣው ሁሉ፤ በርካታ የአለማችን አገራትም በተመሳሳይ ችግሮች ሳቢያ እየተቃወሱ ናቸው። የዩክሬንም ተመሳሳይ ነው። “የራሺያ ተወላጅ”ና “የዩክሬን ተወላጅ” ከሚለው መቧደኛ በተጨማሪ፤ “የኦርቶዶክስ ተከታይ”ና “ወደ ካቶሊክ ያዘነበለ” በሚል የጥላቻ ሰበብ ጭምር ነው፤ ያ ሁሉ የዩራሬይን ችግር እየተፈጠረ የሚገኘው። ቻይና ውስጥ የቲቤት፣ የኡድገር፣ የሃን ተወላጆች በሚል ግጭቶች እየተፈጠሩ ነው። በህንድ ደግሞ፤ ሃይማኖታዊና ብሄረተኛ ግጭቶችን ያነሳሳል ተብሎ ሲወገዝ የነበረ ፓርቲ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየገነነ ዘንድሮ በምርጫ የበላይነት ይይዛል ተብሎ ይጠበቃል።
የጐሰኝነት ወይም የብሄረተኝነት ቀውስ ማለቂያ ያለው አይመስልም። በስልጣኔ ደህና ተራምደዋል የሚባሉ የምዕራብ አውሮፓ አገራትም፤ ከዘመኑ የጎሰኝነት ችግር ማምለጥ የቻሉ አይመስሉም። ስኮትላንድን ከብሪታኒያ ለመገንጠል፣ በሚቀጥለው መስከረም ወር የውሳኔ ሕዝብ ምርጫ ይካሄዳል ተብሏል። በስፔን ደግሞ ካታሎኒያን ለመነጠል  ተመሳሳይ ምርጫ በህዳር ወር ለማካሄድ ታቅዷል። ስኮትላንድ ከብሪታኒያ የምትገነጠልበት፣ ካታሎኒያ ከስፔን የምትነጠልበት አንዳች አሳማኝ ምክንያት ሊኖር ይችላል ብላችሁ ትገምቱ ይሆናል። ግን በብሄር ወይም በጎሳ ከመቧደን የዘለለ ብዙም ምክንያት አይታይም።
ቢሆንም፣ የእንግሊዝ መንግስት በስኮትላንድ የታቀደው ምርጫ እንዲካሄድ ተስማምቷል። የስፔን መንግስት ግን፣ በካቶሎኒያ የታሰበው ምርጫ ህገወጥ እንደሆነ በመግለፅ ምርጫውን እንደሚያግድ አሳውቋል። መገንጠልን የሚደግፉ ፖለቲከኞች ግን፤ ከአላማቸው ፍንክች እንደማይሉና እቅዳቸው እንደማይለወጥ ተናግረዋል። ለበርካታ አመታት የያዙትን አቋም፤ “አሁኑኑ ተግባራዊ ካላደረግን ሞተን እንገኛለን” ማለታቸው ለምን ይሆን? ምላሽ አላቸው። “አንደኛ፤ ስኮትላንድ በአርአያነት እንድንነሳሳ አድርጋለች፡፡ ሁለተኛ ደግሞ ዛሬ እንደ ድሮ አንፈራም። ስፔን የአውሮፓ ህብረት አባል ከሆነች ወዲህ፣ ዲሞክራሲ ተጠናክሮ ነፃነትና መብት የሚከበርባት አገር ሆናለች።  እንታሰር ይሆናል፤ እንገደል ይሆናል የሚል ስጋት ስለሌለን፤ የመገንጠል አቋማችንን ለማሳካት ምርጫውን እናካሂዳለን” ብለዋል- ካታሎኒያን ለማስገንጠል ዘመቻ የሚያካሂዱ ፖለቲከኞች። በአንድ በኩል፣ የፖለቲከኞቹ አባባል ቀጥተኛ ምላሽ ይመስላል። በሌላ በኩል ግን የሚያስገርም ነገር አለው።
አገሪቱ የእያንዳንዱ ሰው መብትና ነፃነት የሚከበርባት ከሆነች፤ መገንጠል ለምን አስፈለገ? የአስተሳሰብ ጉዳይ ነው። ከ17ኛው ክፍለዘመን ጀምሮ፤ ስልጡን የፖለቲካ አስተሳሰብ እየተስፋፋ በነበረበት በ18ኛውና በ19ኛው ክፍለ ዘመን ላይ፤ ማንኛውም የፖለቲካ ውሳኔም ሆነ አቋም፤ ከሁሉም በፊት የእያንዳንዱን ሰው መብትና ነፃነት ለማስከበር ያለመ መሆን አለበት የሚል መርህ ይከበር ነበር። አሜሪካ ከእንግሊዝ እንድትገነጠል ዘመቻ ያካሄዱ እንደ ጀፈርሰንና ማደሶን የመሳሰሉ መስራች ፖለቲከኞችም በዚህ ይስማሙ ነበር። ይህንን መርህ ነው የነፃነት መግለጫ በሚል ስያሜ ባዘጋጁት ሰነድ ውስጥ በጉልህ ያሰፈሩት።
የመገንጠልም ሆነ የመዋሃድ ውሳኔ፤ ለአመፅ የመነሳትም ሆነ የመስማማት ውሳኔ ምክንያታዊ ተቀባይነት የሚኖረው መቼ ነው? የእያንዳንዱ ሰው መብትና ነፃነት እንዲከበር አወንታዊና ጉልህ ውጤት የሚያበረክት ከሆነ ብቻ ነው። በአንዳች ውሳኔ የሚገኘው ውጤት ወይም ለውጥ፣ አወንታዊ መሆኑ ብቻ በቂ አይደለም። ጉልህ ለውጥ ወይም ጉልህ ውጤት የሚያስገኝ መሆን አለበት። ለጥቃቅን ለውጥ ተብሎ፣ ነባሩን ስርዓት ማናጋት ተገቢ እንዳልሆነ የአሜሪካ የነፃነት መግለጫ በአፅንኦት ያሳስባል።
ዛሬ ግን፣ ያ ስልጡን የፖለቲካ አስተሳሰብ ብዙም ትኩረት ሲሰጠው አይታይም። ጭራሽ፤ የመገንጠል አቋማችንን የምናፋጥነው፤ አገሪቱ መብትና ነፃነትን ማክበር በመጀመሯ ነው የሚሉ ፖለቲከኞችን እየሰማን ነው።
የራሺያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ ክሬሚያን በውሳኔ ሕዝብ ከዩክሬን አስገንጥለው የጠቀለሉበት ድራማም ተመሳሳይ ነው። ብዙ ራሺያውያን (ወደ 70 በመቶ ያህሉ) የፑቲንን ድርጊት መደገፋቸው አይደለም አስገራሚው ነገር። የፑቲን ቀንደኛ ተቃዋሚ የሆኑና በዚህም ታስረው የተንገላቱ ፖለቲከኞች ጭምር፤ ክሬሚያ ከዩክሬን ተገንጥላ በራሺያ ስር መግባቷን እንደሚደግፉ ለታይም መፅሔት ገልፀዋል። ለምን? በቃ፤ በክሬሚያ የሚኖሩ አብዛኞቹ ሰዎች የራሺያ ተወላጅ ናቸው። ከዚህ በመቀጠል የተናገሩትን ደግሞ ተመልከቱ።
“በእርግጥ” አሉ አንዷ ቀንደኛ የፑቲን ተቃዋሚ፤ “በእርግጥ፤ የክሬሚያ ነዋሪዎች በውሳኔ ሕዝብ ወደ ራሺያ በመጠቃለላቸው የሚያተርፉት ነገር የለም። እንዲያውም፤ መብትና ነፃነታቸው እንዲከበር የሚፈልጉ ከሆነ ከዩክሬን ጋር መቀጠል ይሻላቸው ነበር። በራሺያ ስር ለመሆን የወሰኑ ጊዜ፣ ከመብትና ከነፃነት ጋር ተለያይተዋል። እንዲያውም ከእንግዲህ በኋላ፤ ውሳኔ ሕዝብና ምርጫ የሚባል ነገር እንደገና የማየት እድል አይኖራቸውም” ብለዋል። በሌላ አነጋገር፤ ክሬሚያ ከዩክሬን የተገነጠለችበትና ወደ ራሺያ የተጠቃለለችበት ውሳኔ፤ የሰዎች መብትና ነፃነት እንዲከበር አንዳችም አወንታዊ አስተዋፅኦ አይኖረውም። እንዲያውም መብትና ነፃነትን የሚያሳጣ ውሳኔ ነው። ይህንን የተናገሩት፤ የፑቲን ቀንደኛ ተቃዋሚ የሆኑት ፖለቲከኛ ናቸው። ግን ደግሞ ውሳኔውን ይደግፋሉ። ዋና መመዘኛቸው፤ “የመብትና የነፃነት” ጉዳይ ሳይሆን፤ የዘር እና የብሔር ተወላጅነት ነው።
በአጠቃላይ፤ ከአፍሪካ እስከ ኤስያ፣ ከደቡብ አሜሪካ እስከ አውሮፓ... አለምን እያመሳቀሉ ከሚገኙት ሶስት ቀውሶች መካከል ሁለተኛው፣ ይሄው የጎሰኝነት ወይም የብሄረተኝነት አባዜ ነው። አንደኛ የሃይማኖት አክራሪነትና ሽብር፤ ሁለተኛ የጎሰኝነትና የብሄረተኝነት አባዜ።
ታይም መፅሔት ባለፈው ሰኞ በሽፋን ገፁ ላይ አጉልቶ ያወጣው ዋና ርዕሰ ጉዳይም፤ በእነዚህ ነጥቦች ላይ ይስማማል። በመፅሔቱ ቅድሚያ ስፍራ ተሰጥቶት የታተመው ፅሁፍ በጥቅሉ፤ “የኋላቀርነት ትርምስና ግጭት - በ21ኛው ክፍለዘመን” የሚል ጭብጥ የያዘ ሲሆን፤  አለማችን ብዙዎች ባልጠበቁት ቀውስ ከዳር ዳር እየተናጋች መሆኗን ይገልፃል። ከብሔረተኝነትና ከሃይማኖት ጋር በተያያዙ ኋላቀር ስሜቶች አማካኝነት በየአገሩና በየአቅጣጫው የሚፈጠሩ ትናንሽና ትላልቅ ግጭቶች፣ ምድሪቱን እያናወጧት ነው። ኋላቀር ግጭትና ማብቂያ በሌለው ትርምስ መበራከቱ መንግስታትንና ባለስልጣናትን፣ ምሁራንና ፖለቲከኞችን ግራ እንዳጋባ የሚተነትነው የመፅሔቱ ሰፊ ፅሁፍ፤ “21ኛው ክፍለዘመን እንዲህ ይሆናል ተብሎ አይጠበቅም ነበር” በማለት ነው የሚጀምረው። ... This isn’t what the 21st century was supposed to look like የሚለው አባባል በተጨባጭ ለማሳየት፣ በዩክሬን፣ በአረብና በአፍሪካ አገራት የተከሰቱ ቀውሶችን እያጣቀሰ ወደ ትንታኔው ይቀጥላል።
ለመፍትሄ ያስቸገረው ሦስተኛ ቀውስ፤ እንዲሁም በእንጥልጥል እየቀሩ ያስቸገሩ ሶስት ምኞቶችን ለሳምንት ላቆያቸው። እስከዚያው፤ ከሁለቱ የቀውስ ምንጮች ለመዳን እየተጋን እንሰንብት።

Monday, 07 April 2014 15:17

ለማይስቅ ውሻ ነጭ ጥርስ

ለማይገላመጥ ዶሮ ቀይ ዐይን ይሰጠዋል!
(የሚጬነ ከናስ አቻ ቦታ እሜስ ዴሬቄነ ኩቶስ አይፌ ዞኡዋ እሜስ)
የወላይታ ተረት

ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ደቃቃ ጥንቸል፤ እህል ውሃ ፍለጋ በጫካ ውስጥ ስትዘዋወር፤ አንድ ዝንጀሮ ታገኛታለች፡፡ ጥንቸሏ ግዙፍ ስላልሆነች በየቅጠላ ቅጠሉ ውስጥ እየተሹለከለከች መሄድ እንደምትችል ዝንጀሮ ያውቃል፡፡ ሆኖም አንድ ምክር ሊመክራት ፈልጓል፡፡
“እመት ጥንቸል! የረዥም ጊዜ ወዳጅነታችንን መሰረት በማድረግ ምክር ልለግስሽ እፈልጋለሁ” አላት፡፡
ጥንቸልም፤
“ምን ዓይነት ምክር? ስትል ጠየቀችው”
ዝንጀሮም፤
“ይህን ጫካ አትመኝው፡፡ ሰሞኑን አዳኞች መጥተው ለአውሬ ማጥመጃ የሚሆን ትላልቅ ጉድጓድ ሲቆፍሩ እኔ ዛፍ ላይ ሆኜ አይቻቸዋለሁ፡፡ ስለዚህ ጫካው እንደድሮው ሰላም መስሎሽ ወዲህ ወዲያ አትበይ”
ጥንቸልም፤
“አመሰግናለሁ፡፡ የወጥመዱን የሰሩት ለእኔ አይመስለኝም፡፡ እንደ አንበሳ፣ እንደነብር፣ እንደዝሆን ላሉት እንጂ እንደኔ ቀጫጫ ለሆነ ፍጡር አይደለም፡፡ ባጋጣሚ ጉድጓድ ውስጥ ብወድቅም መውጫ ብልሃት አላጣም!” ትለዋለች፡፡
ዝንጀሮም፤
“እንግዲህ የወንድምነቴን መክሬሻለሁ፡፡ ብታውቂ እወቂበት” አላትና ሄደ፡፡
ጥንቸል እየተዘዋወረች ቅጠል መበጠሷን ትቀጥላለች፡፡ ጥቂት እንደሄደች ዝንጀሮ እንደፈራው አንድ በቅጠል የተሸፈነ ትልቅ ጉድጓድ ውስጥ ሳታስበው ትወድቃለች፡፡ ጉድጓዱ በጣም ጥልቀት ያለው በመሆኑ በጭራሽ በቀላሉ ልትወጣ የምትችልበት አይደለም፡፡ ስለዚህ አላፊ-አግዳሚውን እንዲያወጣት ለመለመን ተገደደች፡፡
“እባካችሁ አውጡኝ፡፡ እባካችሁ እርዱኝ!” እያለች መጮህ ጀመረች፡፡ ተኩላ ድምጿን ይሰማና ወደ ጉድጓዱ አፍ ይሄዳል፡፡ አጎንብሶም ወደ ጥንቸሏ ያይ ጀመር፡፡
ጥንቸልም
“አያ ተኩላ! እባክህ ዘወር በል፡፡ ይሄ ጉድጓድ ለሁለታችን አይበቃንም፡፡ አንተ ያለህበት ቦታ እንደበረሀ የሚያቃጥል አየር ነው ያለው፡፡ እዚህ ግን በጣም ነፋሻና ቅዝቅዝ ያለ አየር ነው ያለው፡፡ ለእኔ በጣም ተስማምቶኛል፡፡ ሆኖም ወደዚህ ለመውረድ ብትችልም እንኳን ቦታው አይበቃንም” አለችው፡፡ ተኩላ፤ የጥንቸሏ ንግግር በጣም አጓጓውና፤ “ልውረድስ ብል በምኔ እወርዳለሁ?” ሲል ጠየቃት፡፡
ጥንቸልም
“እዚያ ጉድጓድ አፍ አጠገብ አንድ በገመድ የታሰረ ባሊ አለልህ፡፡ ባሊው ውስጥ ገብተህ በገመዱ ተንሸራተህ መውረድ ትችላለች” አለችው፡፡
ዕውነትም አንድ ባሊ አጠገቡ እንዳለ አየ፡፡ ባሊው ወደታች ሲወርድ ጉድጓዱ ውስጥ ያለው ገመድ ጫፍ ወደላይ የሚወጣ ነው፡፡ እንደ ፑሊ የሚሰራ ገመድ ነው፡፡ ጉድጓድ ውስጥ ያለውን ጫፍ ጥንቸሏ ይዛለች፡፡
አያ ተኩላ ባሊው ውስጥ ገብቶ ቁልቁል ተምዘግዝጎ ሲወርድ ጥንቸል የገመዱን ጫፍ ይዛ ወደ ላይ መጣች፡፡
እሱ እየወረደ፣ እሷ እየወጣች መንገድ ላይ ሲተላለፉ፤ ከት ብላ እየሳቀች፤
“አየህ አያ ተኩላ፤ ህይወት ማለት እንደዚህ ናት፡፡ አንዱ ሲወርድ አንዱ ይወጣል!“ አለችው፡፡
ተኩላ መሬት ሲደርስ ጥንቸሏ ጉድጓዱ አፋፍ ወጣች!
*   *   *
አንዳንድ ሰዎች አንድ ችግር ውስጥ ሲገቡ ሌላውን እዚያ ውስጥ ነክረው እራሳቸውን ማዳን ይችሉበታል፡፡ ተታልለው እዚያ ችግር ውስጥ የሚገቡት ሞኞች የሚሳሳቱት በአልጠግብ ባይነታቸውና እጉድጓዱ ውስጥ እንኳ ያለው ነገር እንዳያመልጠኝ ብለው ሲስገበገቡ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት በርካታ ሰዎች ጉድጓድ ውስጥ ገብተው ቀርተዋል፡፡ ዞሮ ዞሮ ሁለቱም ለሀገርና ለህዝብ አይጠቅሙም፡፡ አደጋን ከሩቅ አይተው የሚያስጠነቅቁ እንደ ዝንጀሮው ያሉ አስተዋዮች ቢኖሩም እህ ብሎ የሚያዳምጣቸው ሰው አያገኙም፡፡ ባንዱ እግር ሌላው እየገባ፣ ህይወት ትቀጥላለች፡፡
ማይ ግሪንፊልድ የተባለ ፀሐፊ፤
“ታሪክ ራሱን ይደግማል፤ ይላል ታሪከኛ ሁሉ
እኔን ያሳሰበኝ ግና፣
ታሪክ በደገመ ቁጥር፣ ዋጋው ይብስ መቀጠሉ” ይላል፡፡ የሚያስከፍለን ዋጋ እየባሰ የሚመጣው እኛ ከታሪክ ለመማር ባለመቻላችን ነው፡፡ የቀደመው የሰራውን ስህተት የኋለኛው ይደግመዋል - ያውም በዚያኛው እየሳቀ፣ እየተሳለቀ! “በእገሌ ጊዜ የተበደላችሁ እጃችሁን አውጡ!” እያለ፡፡ ከንቲባዎች ተቀያረዋል፡፡ አስተዳዳሪዎች ተቀያይረዋል፡፡ ሚኒስትሮች ተቀያይረዋል ወዘተ… ማንም ከማንም አይማርም፡፡ ሁሌ እኔ ከወደቀው የተሻልኩ ነኝ የሚለውን ለማረጋገጥ የቀደመውን እየረገሙ መቀጠል ነው!! በዚህ ዓይነት ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት እመሰርታለሁ ብሎ ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ ከተነሳው ሹም መውሰድ ያለብንን ደግ ነገር ካላወቅን ከዜሮ እንደ መጀመር የከበደ ነው ጉዟችን፡፡
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት ጀርመኖች ለንደንን በቦምብ በደበደቡ ጊዜ ሦስት ዓይነት ህዝቦች ተፈጥረው ነበር ይባላል፡፡ 1) የተገደሉ 2) ለጥቂት የተሳቱና 3) በርቀት የተሳቱ፡፡ የተገደሉት ሟቾች ናቸውና ስለአደጋው ወሬ አይነዙም፡፡ ለጥቂት የተሳቱት በሰቀቀንና ስቃዩን በማስታወስ የሚኖሩ ሆኑ፡፡ በሩቅ የተሳቱት ግን ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖቹን ለመዷቸውና ልበ ሙሉ ሰዎች ሆኑ፤ ይለናል ፀሐፊው ማልኮልም ግላድዌል፡፡ ችግርን መልመድ ደፋርና ልበ - ሙሉ ያደርጋል ነው ነገሩ! ከዚህ ተነስቶ ለአገርና ህዝብ መቆርቆር መቻል መታደል ነው፡፡ በዚህ ወቅት ደሞ ማየት፣ በትክክለኛው ቦታ መገኘትና የሚሰሩትን በቅጡ ማወቅ ግዴታ ነው፡፡ ችግርን ለምዶ መተኛት ግን ሌላ ችግር ነው! ሁሉ በጄ ሁሉ በደጄ እያሉ አግባብነት ያለው ተግባር የማይፈፅሙ አያሌ ናቸው፡፡ የተማሩትና የሰለጠኑበት ሌላ የሚሰሩት ሌላ፤ የሆኑም አያሌ ናቸው! ስለግንባታ እያወሩ የማይገነቡ ከአፈረሰ አንድ ናቸው፡፡ መንገድ ሰርቶ በቅጡ ሳንሄድበትና ሳናጣጥመው ከፈረሰ ወይ ሰሪው በቅጡ አላበጀውም፣ ወይ ሂያጆቹ መሄድ አይችሉም፣ አሊያም ሆነ ብለው የሚያጠፉ አሉ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ በቅጡ ራስን መመርመር ያስፈልጋል፡፡ “የነቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንበሌጥ”ንም ልብ ማለት መልካም ነው፡፡ ሁሉን በውል በውሉ ካላስቀመጥንና ታማኝነትን ብቻ መለኪያ እናድርግ ካልን የተወዛገበ አካሄድ ውስጥ እንሰረነቃለን፡፡ እመጫት እንደ በዛው ፅሁፍ ከዋናው ማረሚያው ይበረክታል፡፡ ከተቃወምንም ዕድሉን ባግባቡ እንጠቀም፡፡ እንዳያማህ ጥራውንም እንተው! በእጃችን ያለውን በወጉ መጠቀም ያስፈልጋል በሁሉም ወገን፡፡ አለበለዚያ “ለማይስቅ ውሻ ነጭ ጥርስ፣ ለማይገላምጥ ዶሮ፣ ቀይ ዐይን ይሰጠዋል” የሚለው የወላይተኛ ተረት ይመጣል፡፡ “ቆሎ ለዘር፤ እንዶድ ለድግር አይሆንም” እንደሚባለው ማለት ነው፡፡    

Published in ርዕሰ አንቀፅ

 

  •  “መንግስት መረጃን በሞኖፖል በያዘበት ወቅት፣ስለ ፕሬስ ነፃነት ማውራት አይቻልም”   ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ
  • “ጋዜጦች የሀብታም መሆናቸው ቀርቶ ድሃ ተኮር የሚሆኑበትን ስልት መንደፍ ያስፈልጋል”  ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ
  • “የጋዜጣ ኢንዱስትሪው አልተዳከመም፤አዳዲስ ጋዜጦች እና መፅሔቶች እየታተሙ ነው”   አቶ አንተነህ አብርሃም

         ከ1980ዎቹ አጋማሽ ጀምሮ የጋዜጣ ደንበኛ እንደሆኑ ይናገራሉ -አቶ ያለው ደግፌ፡፡ በተለይም የግል ፕሬስ ውጤቶችን ሳያሰልሱ ያነቡ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ ኢህአዴግ ሀገሪቷን ከተቆጣጠረና የነፃ ፕሬስ አዋጅን ካወጀ በኋላ፣አብዛኞቹ ጋዜጦች ትኩረታቸውን ወደ ፖለቲካና አገራዊ ጉዳዮች ማድረጋቸውን አቶ ያለው ያስታውሳሉ። በተለይ ከኤርትራ መገንጠል፣ ከደርግ ውድቀት፣ ከፌደራሊዝም ስርአቱ ብሄር ተኮር መሆን ጋር የተያያዙ ጉዳዮች በእነዚህ ጋዜጦች በስፋት ይዳሰሱ ነበር፡፡ ጋዜጦቹ ፍራቻ እንዳልነበረባቸው ለመዳሰስ የሚያነሷቸው ጠንካራና አይነኬ የሚመስሉ ጉዳዮች ማሳያ ናቸው - ይላሉ፣የረጅም ጊዜ የጋዜጣ አንባቢው አቶ ያለው፡፡
የጋዜጦች ዋጋም ኪስ የማይጎዳ እንደነበርና የአንድ ጋዜጣ ዋጋ ከ75 ሳንቲም እንደማይበልጥ ያስታውሳሉ፡፡ አብዛኛው አንባቢም ጋዜጣ ገዝቶ የማንበብ ልማድ ነበረው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ነገሮች ተለውጠዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን በ2005 ዓ.ም ባወጣው የዳሰሳ ጥናት ላይ እንደተመለከተው፤የህትመት ዋጋ ንረት በፈጠረው ተፅዕኖ፣ ጋዜጣን ገዝቶ ከሚያነበው ይልቅ ከአዟሪዎች በኪራይ የሚያነበው ይበልጣል፡፡ በጥናቱ ከተካተተው ጠቅላላ አንባቢ አብላጫው /35.24 በመቶ ያህሉ/  ተከራይቶ ሲያነብ፣በሁለተኛነት /32.75 በመቶው/ ገዝቶ ያነባል፡፡ የተቀረው በመስሪያ ቤት በኩል በቤተ መጻሕፍት እና በተለያዩ መንገዶች እንደሚያነብ ጥናቱ ይጠቁማል፡፡ ያነጋገርናቸው አንዳንድ አዟሪዎች በበኩላቸው፤በኪራይ ንባብ ብቻ በቀን ከ70 ብር በላይ ገቢ እንደሚያገኙ ጠቅሰዋል፡፡ በ1998 ዓ.ም የአንድ ጋዜጣ መሸጫ ዋጋ 2ብር ከ50 የነበረ ሲሆን በ8 ዓመት ውስጥ በ4 እጥፍ ጨምሮ አሁን በ10 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
የሽግግር ወቅቱ የፖለቲካ መስመሮች ያልጠሩበት መሆኑ ለጋዜጦች መስፋፋት አስተዋፅኦ አበርክቷል የሚል እምነት እንዳላቸው የሚናገሩት አቶ ያለው፤ በዚያው ልክ ጋዜጦቹ ፅንፈኝነት፣ ዘረኝነትና ጥላቻ በህብረተሰቡ ውስጥ ቦታ እንዲኖራቸው አድርገዋል ሲሉ ይተቻሉ፡፡ በተቃራኒው ስለ ሀገር አንድነትም የሚወተውቱ ጋዜጦች እንደነበሩ ያስታውሳሉ፡፡ ከእነዚህ ጋዜጦች መካከል በሐምሌ እና ነሐሴ 1985 ዓ.ም ወደ ገበያው የተቀላቀሉ “ጦማር” እና “ጥንቅሽ” ጋዜጦችን ጨምሮ በ1986 ዓ.ም ወደ ስርጭት የገቡት “መብረቅ”፣ “ሞገድ”፣ “ሰይፈነበልባል”፣ “አዕምሮ”፣ “ኢትዮጵ”፣ “ጎዳናው”፣ “ጦቢያ”--- በወቅቱ ተነባቢነት የነበራቸው ጋዜጦች ናቸው፡፡ ከእነዚህ ጋዜጦች መካከል ከሁለት እና ሶስት ዓመት እድሜ ያልዘለሉ ቢኖሩም አብዛኞቹ ሥርዓተ ፍፃሜያቸው የተከናወነው ግን በምርጫ 97 ማግስት ነው፡፡
በፖለቲካ ጉዳይ ላይ ብቻ አተኩረው እስከ 1998 ዓ.ም ሲታተሙ ከቆዩት የግል ጋዜጦች መካከል “ልሣነ-ህዝብ”፣ “ሐዳር”፣ “ምኒልክ”፣ “ሩህ”፣ “ሣተናው”፣ “ነፃነት”፣ “አስኳል”፣ “አዲስ ዜና”፣ “ክብሪት”፣ “እለታዊ አዲስ”፣ “ጎህ” እና “ዘ ፕሬስ” ተጠቃሾች ናቸው፡፡ እነዚህም ቢሆኑ የበረከቱት እስከ 1998 ዓ.ም ብቻ ነው፡፡ እነዚህን ጨምሮ 23 ጋዜጦች ያህል የተዘጉት በምርጫው ማግስት በማተሚያ ቤቶች አናትምም ባይነት ነበር፡፡ እስከ 1997 ዓ.ም ድረስ ወደ 106 የሚደርሱ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩ ጋዜጦች እየታተሙ ለገበያ ይቀርቡ ነበር፡፡    
ፖለቲካዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ከሚያተኩሩት ጋዜጦች ባሻገር፣ወሲብና ስነ-ወሲብን እንዲሁም ፍቅርና ፆታዊ ጉዳዮችን የሚዳስሱ ጋዜጦች ከ1987 ጀምሮ እስከ 1990ዎቹ አጋማሽ እንደ አሸን ፈልተው ነበር፡፡ “ኤሮቲካ”፣ “እውነተኛ ፍቅር”፣ “የፍቅር ህይወት”፣ “የፍቅር ማህደር”፣ “የፍቅር ረመጥ”፣ “የፍቅር ጨዋታ”፣ “ፍቅረኞች”፣ “ፍቅር”፣ “ማዶና” ወዘተ--- የተሰኙት ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ከእነዚህ መካከል አብዛኛዎቹ በ1990ዎቹ አጋማሽ በህዝብ ተቃውሞ እንዲታገዱ ተደርገዋል። እንዲያም ሆኖ ተወዳጅ እንደነበሩ የሚናገሩም አሉ። ከእነዚያ ጋዜጦች የአንደኛው አዘጋጅ ሲናገሩ፣ ከመወደዳቸው የተነሳ ከዋጋቸው በላይ እስከ 10 ብር ይሸጡ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ የፍቅርና ወሲብ ጋዜጦች የአንባቢውን የትኩረት አቅጣጫ በማስቀየር ረገድም የተሳካላቸው ነበሩ የሚሉት አዘጋጁ፤በዚህም ምክንያት የፖለቲካ ጋዜጦች ገበያ መቀዛቀዝ አሳይቶ እንደነበር ያወሳሉ፡፡ ጋዜጦቹ በ1990ዎቹ አጋማሽ በህዝብ ተቃውሞ መዘጋታቸው ለፖለቲካ ጋዜጦች ገበያ መጨመር ትልቅ አስተዋፅኦ አድርጓል።
በአገሪቱ የፕሬስ ታሪክ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ጋዜጦች የታተሙት በምርጫ 97 ወቅት ሲሆን ከ100 ሺህ በላይ ቅጂዎች የሚያሳትሙ ነበሩ። አንድ ጋዜጣ በቀን ሁለት እና ሶስት ጊዜ እስከ መታተም ደርሶ እንደነበረም መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በአሁን ወቅት ግን ከፍተኛው የቅጂዎች ብዛት በአማካይ ከ10 ሺህ ኮፒ እንደማይበልጥ የብሮድካስት ባለሥልጣን ጥናት ይጠቁማል፡፡
ድህረ ምርጫ 97 እና የግሉ ፕሬስ
ከ1999 እስከ 2005 ባለው ጊዜ ውስጥ የአንባቢን ትኩረት አግኝተው ከነበሩት ከ22 በላይ በአማርኛ ቋንቋ የሚታተሙ ጋዜጦች መካከል በአሁን ወቅት በገበያው የቀሩት 6 ጋዜጦች ብቻ ናቸው፡፡ በዘንድሮ ዓመት  ወደ ገበያው የገቡት ደግሞ በሰማያዊ ፓርቲ የሚታተመው “ነገረ-ኢትዮጵያ” እና ከተጀመረ ሳምንታት ያስቆጠረው “አፍሮ-ታይምስ” ናቸው፡፡ እንደ ሰማያዊ ፓርቲ ጋዜጣ ሁሉ መኢአድ “አንድነት” የሚል፣ አንድነት ፓርቲ ደግሞ “ፍኖት ነፃነት” የተሰኘ ልሳናት ያሳትሙ የነበረ ቢሆንም በማተምያ ቤት ችግርና በሌሎች ምክንያቶች ከህትመት ውጭ ሊሆኑ በቅተዋል፡፡
የግል ፕሬሱ ለምን ተዳከመ?
ለጋዜጦች መዘጋት የህትመት ዋጋ ንረት ቀዳሚውን ስፍራ እንደሚይዝ የተለያዩ የጋዜጣ ባለቤቶች ይናገራሉ፡፡ በአንድ ወቅት በገበያው ጥሩ ተፎካካሪ ከነበሩት መካከል “አዲስ-ነገር” ጋዜጣን የመሳሰሉት ደግሞ ምንም አይነት የፋይናንስ ችግር ባይገጥማቸውም አዘጋጆቹ “ከመንግስት ጫና ተደረገብን” በሚል ምክንያት ዘግተው ከአገር ተሰደዱ፡፡
የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን የ2005 ጥናት፣የጋዜጦች ድክመቶች ተብለው ከተጠቀሱት መካከል በየጊዜው ዋጋ መጨመራቸውና የተደራሽነት ክፍተት ይገኙበታል፡፡ በጥናቱ ተሳታፊዎች ከተጠቆሙ የማሻሻያ ምክረ ሀሳቦች (recommendation) መካከል፣ፕሬሶች ፍራቻን አስወግደው በትክክለኛ መረጃዎች ላይ የተመሰረቱ ዘገባዎችን ለህብረተሰቡ በነፃነት ቢያቀርቡ፣የህትመት ዋጋን ለመቀነስ የሚያስችል ሁኔታ ቢፈጠር፣ እና መንግስት ዘርፉን የሚያበረታታ የፖሊስ እርምጃ ቢወስድ የሚሉት ይጠቀሳሉ፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሚዩኑኬሽን ትምህርት ክፍል ምክትል ኃላፊ ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ በበኩላቸው፤የሃገራችን የግል ጋዜጦች ሮጠው ሳይጠግቡ ግብአተ መሬታቸው ለመፈፀሙ ምክንያት ያሏቸውን ይጠቅሳሉ። ጋዜጦቹ ሰፊውን ህዝብ ተደራሽ ያላደረጉ መንደረኛ ባህሪ ያላቸው ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ብቻ ማተኮራቸው፣ ሚዛናዊ ባለመሆናቸው የእነ እከሌ ጋዜጣ ነው እስከመባል በሚያደርሱ ፍረጃ ውስጥ ራሳቸውን ከተው መገኘታቸው እንዲሁም የበሰለ ሙያዊ መሰረት የሌላቸው ወይም በትክክለኛው ባለሙያ ያለመዘጋጀታቸው ለጋዜጦቹ ውድቀት መፍጠን አስተዋፅኦ ካበረከቱ ጉዳዮች ተጠቃሽ እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡ በመንግስት ስርአት ውስጥም ገና በዲሞክራሲ ግንባታ ሂደት ላይ መገኘቱ በራሱ ሚዲያውም በሙያ ለመዳበር፤ይበልጥ ነፃና ለብዙሃን ተደራሽ መሆን ላለመቻሉ አስተዋፅኦ ማበርከቱን ዶ/ር ነገሪ ገልፀዋል፡፡
ከምርጫ 97 በፊት የነበሩት ጋዜጦች ልክ የፕሬስ ነፃነት ሲታወጅ መብቱ ምን ድረስ ነው የሚለውን ከግንዛቤ ባለማስገባት፣ራሳቸውን የመንግስት ተቃዋሚ አድርገው እስከመፈረጅ መድረሳቸውን የሚጠቅሱት ሌላው ስሜ አይጠቀስ ያሉ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነት መምህር፤በወቅቱ የፅንፈኝነት ባህሪ ማንፀባረቃቸው ለውድቀታቸው ዋነኛው መንስኤ እንደነበር ይጠቅሳሉ፡፡ ከዚያ በኋላ ወደ ገበያው የተቀላቀሉ አንዳንድ የፕሬስ ውጤቶችም በዘገባ አሰራር ስነ-ልኬት በሚገባ ያልዳበሩ በመሆናቸው፣ ራሳቸውን መከላከል በማይችሉበት ሁኔታ ለመንግስት ጫናና አፈና እንደተዳረጉ እኚሁ ምሁር ያስረዳሉ፡፡ በፋይናንስ እጥረት እስከ መዘጋት የደረሱ ጋዜጦች መኖራቸውን እንደሚያውቁ የጠቆሙት ምሁሩ፤የፋይናንስ ችግሩም የህትመት ዋጋ ንረቱም ሆነ ተያያዥ ጉዳዮች በመንግስትና በግሉ ፕሬስ መካከል የቆመው ሊታረቅ ያልቻለ የፅንፈኝነት ሃውልት ውጤት ናቸው ይላሉ፡፡
ዶ/ር ነገሪ በበኩላቸው፤ በቅድመ 97 ምርጫ ይታተሙ የነበሩ አንዳንድ ጋዜጦች አሁን በስልጣን ላይ ያለውን መንግስት “ህጋዊ መንግስት አይደለም፣ ሰርቆ የመጣ ነው” የሚሉ ዘለፋዎችን መጠቀማቸው ለፖለቲካዊ ጫና ዳርጓቸዋል ይላሉ፡፡ ሙያው ገና ባልዳበረበትና ስልጣን ላይ ያለው መንግስት አብዮታዊ ዲሞክራሲ ርዕዮት ዓለም አራማጅ ሆኖ ሳለ፣ ሚዲያዎች የሚገባውን ብስለት ተጠቅመው ባለመስራታቸው ዋጋ አስከፍሏቸዋል ብለዋል - ዶ/ር ነገሪ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ በመንግስት የተረቀቀውና ተግባራዊ የተደረገው የፀረ-ሽብር አዋጅ ይበልጥ በመንግስትና በግል ፕሬስ መካከል አለመተማመን መፍጠሩን ዶ/ር ነገሪ አስረግጠው ይናገራሉ፡፡ ይሁን እንጂ የሃገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ የፈጠረው ህግ ስለሆነ፣ሚዲያዎች የኢትዮጵያ ሚዲያ እንደመሆናቸው ምዕራባዊያኑን ሳይሆን ኢትዮጵያን መምሰል እንዳለባቸው ይመክራሉ፡፡
በቀጣይም ቢሆን ይበልጥ የግል ጋዜጦች እንዲያብቡ ሰፊ ስራ መሰራት አለበት የሚሉት ዶ/ር ነገሪ፤ ጋዜጦች የገፅ ብዛታቸውን በመቀነስ የዋጋ ትመናቸው ዝቅ እንዲል በማድረግ፣ የሀብታም መሆናቸው ቀርቶ ድሃ ተኮር የሚሆኑበትን ስልት መንደፍ ያስፈልጋል ይላሉ፡፡ ጋዜጦች በውስን ከተሞች ብቻ እንደሚነበቡ የጠቀሱት ምሁሩ፤ይህም የሚያሳየው ሰፊውን ህዝብ ተደራሽ አለማድረጋቸውንና ሃገር አቀፍ ባህሪ አለመላበሳቸውን ነው ይላሉ፡፡
አሁን በገበያ ላይ ያሉትንም ፕሬሶች ከውድቀት ለመታደግ እንዲሁም አዲስ የሚፈጠሩትን ተስፋ ለማለምለም የህብረተሰቡ የማንበብ ባህል መዳበር አለበት የሚሉት ዶ/ር ነገሪ፤ ህብረተሰቡ ጋዜጣ ገዝቶ ሲያነብ፣ ገንዘቡን ከምግብ በላይ ለሆነ የእውቀት ግብይት እንዳወጣው መገንዘብ አለበት ይላሉ፡፡ “ዘርፉ ሙያውን በሚያውቁትና በተማሩት ዜጎች ቢያዝ የበለጠ አዋጭ ይሆናል፣ ማደግም ይችላል” የሚሉት ዶ/ሩ፤ “በርዕሰ ጉዳይ መረጣ ወቅትም ከመንደርተኝነት ይልቅ ሃገራዊ ጉዳይ ላይ ትኩረት ቢያደርጉ ተመራጭ ነው” ሲሉ ይመክራሉ፡፡
“መንግስት መረጃን በሞኖፖል በያዘበት ወቅት ስለ ፕሬስ ነፃነት ማውራት አይቻልም” የሚሉት ደግሞ የፍልስፍና ምሁሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ናቸው፡፡
መንግስት መረጃን በስስት አንቆ በያዘበት ሁኔታ እነዚህ ሁሉ ሚዲያዎች ብልጭ ብለው በቅፅበት ቢጠፉ የሚያስደንቅ አይደለም የሚሉት ዶ/ር ዳኛቸው፤አሁን በህይወት መቆየት የቻሉት ጋዜጦችም ቢሆኑ በብዙ መዳከር መረጃ ለማቅረብ የሚታትሩት ብቻ ናቸው ብለዋል፡፡ ለምሳሌ አንድ ጋዜጣ በህዳሴው ግድብ ዙሪያ የበሰለ ዘገባ ሊሰራ ቢፈልግ፣የግል በመሆኑ ብቻ መረጃው ተቆንጥሮ ለቅምሻ ያህል አሊያም በተንዛዛ ውጣ ውረድ ለማግኘት ይገደዳል፡፡ የራሱ የፕሬሱ ድክመቶች ብለው የዘረዘሯቸውም አሉ፡፡ ነፃ ፕሬሱ ክህሎት ባላቸው ሰዎች የተደራጀ አለመሆኑ፣ ጋዜጣን ፅንፍ ለመያዝ እና ግለሰቦችን ለመስደቢያነት መጠቀም የሚሹ አካላት መኖራቸው--በማለት፡፡
“ስልጡን የሆነ ነፃ-ፕሬስ እንዲኖር ስልጣን ላይ ያለው መንግስት የሚያራምደው ርዕዮተ ዓለም አይፈቅድም” የሚሉት ዶ/ር ዳኛቸው፤ “ደርግ በግልፅ አትናገር ይላል፤ይኸኛው ደግሞ የጋዜጠኝነት ትምህርት ክፍልን ከፍቷል፣በህገ-መንግስቱም የመናገር ነፃነትን ደንግጓል፣ በእርግጥ ይህ ድንጋጌ እየተተገበረ ነው ወይ የሚለው ለኔም ጥያቄ ነው” ብለዋል፡፡ ጋዜጦች ተደራሽነታቸው ጨምሮ ይነቃቁ ዘንድም መረጃን ያለ ስስት መለገስ፣ ክህሎቱ ያላቸው ባለሙያዎች ወደ ዘርፉ እንዲገቡ ማበረታታት ያስፈልጋል ሲሉ ዶ/ር ዳኛቸው አስረግጠው ይናገራሉ፡፡
 የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጋዜጠኞች ህብረት ፕሬዚዳንት አቶ አንተነህ አብርሃም፤ ፕሬሱ እየተዳከመና እየጠፋ ነው የሚለው አያስማማኝም ባይ ናቸው፡፡ የብሮድካስት ኤጀንሲ፣ የፕሬስ ፈቃድ ጠያቂ ቁጥር እጅግ እየጨመረ መሆኑን እየገለፀ ነው ያሉት አቶ አንተነህ፤ የጋዜጣ ኢንዱስትሪው አልተዳከመም በማለት ለማነቃቃት ይሞክራሉ፡፡ ምክንያታቸውን ሲጠቅሱም፣ አዳዲስ ጋዜጦች እና መፅሔቶች በብዛት እየታተሙ ዘርፉን እየተቀላቀሉ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ “አዳዲስ ጋዜጦችና መጽሔቶች ወደ ገበያው መቀላቀላቸውም ዘርፉ ይበልጥ እየፋፋ ነው ያስብላል” የሚሉት የህብረቱ ፕሬዚዳንት፤“ይህ ሂደት የሚቀጥለው ምን አልባት እስከ ምርጫ 2007 ድረስ ሊሆን ይችላል፤ ከዚያ በኋላ እየተቀዛቀዘ ይጠፋ ይሆን? እሱን አብረን የምናየው ይሆናል” ብለዋል፡፡
ጋዜጦች የገበያ ችግር እንዳለባቸው የጠቀሱት የማህበሩ ፕሬዚዳንት፤ መንግስት ሚዲያውን ከማስታወቂያ፣ ከገበያና ከስርጭት አንፃር መደገፍ እንዳለበት ያሳስባሉ፡፡ የወረቀትና የቀለም ዋጋ ንረት እንዲሁም  የምንዛሬ እጥረት የዘርፉ ማነቆዎች እንደሆኑ ጠቅሰው፤ከአንባቢያን አንፃርም ገዝቶ ከማንበብ ይልቅ ተውሶ ማንበብ ባህል እየሆነ መምጣቱ የዘርፉ ፈተና ነው ብለዋል - አቶ አንተነህ።
በመቋቋም ሂደት ላይ ያለው “የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ” ሊቀመንበር አቶ በትረ ያዕቆብ በበኩላቸው፤ የህትመት ውጤቶች ላይ ከመንግስት ከሚደርስባቸው ጫና ባሻገር፣ በንግድ ስርአቱም ለጫና ተዳርገዋል ይላሉ፡፡ “የኢኮኖሚ ችግር ከመንግስት ጫና ጋር ተደማምሮ አብዛኛዎቹን ጋዜጦች ለመዘጋት አብቅቷቸዋል” ያሉት ሊቀመንበሩ፤በቅርቡ በአንድ መጽሄት ላይ የደረሰውን ተመሳሳይ ውድቀት ጠቅሰው፣ ብዙዎቹም ለስደትና ለጉስቁልና ኑሮ ተዳርገዋል ባይ ናቸው፡፡ ወደፊት ማህበራቸው በሁለት እግሩ መቆም ሲችል፣እነዚህን ችግሮች በሂደት ለመፍታት እንደሚጥሩም አቶ በትረ ተናግረዋል፡፡

Page 13 of 13