Saturday, 28 March 2015 09:14

የግጥም ጥግ

የተነሳህ ለት

የዛፍ ባላጋራ
ከምትተናነቅ
ከመቶ ቅርንጫፍ
ከሺህ ቅጠል ጋራ
እንደጡንቻ ሁሉ
ስልት በማፈርጠም
ወርደህ ከግንዱ ጋር
አንድ ለአንድ ግጠም፡፡

ሠም እና ሠም

አበባው አብቦ ንቡ ገብቶልህ
እንግዲህ ጎበሌ ማር ካላበላህ
“እንኳንስ ማርና አላየሁም ሰፈፍ”
እያልህ በመራራ ዜማ ከመንሰፍሰፍ
ያ! የቀፎው አውራ ማሩን የደበቀው
ንብ ሆኖ ሲመጣ ጭስ ሆነህ ጠብቀው፡፡
(“የአመድ ልጅ እሳት” የግጥም መድበል፤
መጋቢት 2007)

Published in የግጥም ጥግ

“…እና ከመሀል ልጀምርላችሁ”
አንድ ሙዚቃ ከፈትኩኝ፡፡ ሙዚቃውን ላፕቶፕ ላይ ተጭኖ ነው ያገኘሁት፡፡ ላፕቶፑ ደግሞ ተሰብሮ የተጠገነ ነው፡፡ የሰበርኩትም እኔ ነኝ፤ ያስጠገንኩትም እኔ ነኝ፡፡ ካስጠገንኩት በኋላ እየወደድኩት መጣሁ። በፊት እጠላው ነበር፡፡ ጊዜዬን ስለሚያባክንብኝ…መጥፎ ፊልሞች ሳይበት እንድውል ስለሚያደርገኝ…ከመፅሐፍት ጋር ሊነጣጥለኝ ደባ ይሸርባል ብዬ በስህተትም ቢሆን ስለማምን ወዘተ…፡፡ እየናቅሁት ስሸከመው ቆይቼ አንድ ቀን እብደት ያባውን ሆድ ብቅል አወጣው፡፡ ላፕቶፔን ሰበርኩት፡፡
ሰብሬው የተገላገልኩ መስሎኝ ነበር፡፡ ሳምንት ሳያልፍ እነዚያ ያስጠሉኝ ፊልሞች ይናፍቁኝ ጀመር። በላፕቶፑ ምክንያት የተራራቅኋቸው መፅሐፍት…ብርቅ የሆኑብኝ ስርቃቸው እንጂ ሳቀርባቸው ይሰለቻሉ፡፡ በተለይ አዳዲስ ሽፋን ያላቸው መፅሐፍት… የፊደሎቻቸው ጠረን አላስቀርብ አለኝ። በሰለቹኝ መጠን ሰባራው ላፕቶፔ ይናፍቀኝ ጀመር።
ስለዚህ ለመስበር አንድ ደቂቃ ያልፈጀው ተግባር ለመጠገን ብዙ ወራትን ወሰደ፡፡ ብዙ ገንዘብም አስወጣኝ፡፡ ከሀኪም ቤት ወጥቶ ቤቴ ሲገባ ላፕቶፑ ከጦር ሜዳ ቆስሎ የመጣ ወንድሜን ይመስለኝ ጀመር፡፡ በጥንቃቄ እየከፈትኩ፣ በጥንቃቄ እየዘጋሁ አስተኛው ጀመር፡፡ ጉረኛነቱ ቀንሷል፡፡ ሳይሰበር በፊት “አቅሜ አይችልም፣ አራዳ ነኝ” እያለ ያናፋ ነበር፡፡
እና ከእለታት አንድ ቀን ከበሽተኛ እንቅልፉ ቀሰቅሼ ሙዚቃ እንዲከፍት ጠየቅሁት፡፡ ማዘዝ ድሮ ቀርቷል፡፡ በፍጥነት ካዘዝኩት ፈዞ ይቀራል። ስለዚህ ጠየቅሁት፡፡ አይዞህ አትቸኩል… ቀስ ብለህ… “Take five” እያልኩ… በቀላል ጃዝ አስመስዬ ረቂቅ ሙዚቃ እንዲከፍትልኝ አዘዝኩት። እና ከዚህ በፊት ያልሰማሁትን ሙዚቃ ከፈተልኝ፡፡
ሙዚቃ ከቅርብ አመታት ወዲህ ብዙም ግድ የማይሰጠኝ ነገር ሆኖብኝ ቆይቻለሁ፡፡ ነብሴ ከጆሮዬ ርቆ ተደብቆ ነበር፡፡ በተለይ ሙዚቃ የማጫወት ስልጣን ለሁሉም ግለሰብ እና በሁሉም ስፍራ እንዲባልግ ከተኮነንን ወዲህ፣ ጆሮዬ የጩኸት ፍሳሽ ማስወገጃ መሳሪያ እንጂ ከነብሴ ጋር ምንም አይነት ግንኙነት እንዳይኖረው አድርጌ ደፍኜዋለሁ። ጆሮ ጩኸትን የሚያስገባ እና ምንም የማድመጥ ሙከራ ሳያደርግ የሚያስወጣ ነገር ሆኗል ለኔ፡፡
ጆሮዬን ወደ ጉበት ቀይሬው ቆይቻለሁ። የድምፅ መርዝ ነፍሴንም ሆነ አእምሮዬን እንዳይጐዳ እንደአገባቡ ማስወጣት ብቻ ነበር የየውሎ አላማዬ።
ምናልባት ላፕቶፕ ከመሰበሩ በፊት በላዩ ላይ የተጫኑትን በሙዚቃ ስም የተሰየሙትን ፋይሎች ለመክፈት ሙከራ የማላደርገው በራሴው እጅ ራሴኑ እንዳልጐዳ ስለምፈራ ሳይሆን አይቀርም። ግን አስታውሳለሁ መጠጥ ጠጥቼ ስሰክር ብቻ ጩኸቶቹን በጆሮዬ ላይ ያሻቸውን እንዲሆኑ ነፃ እለቃቸው ነበር፡፡ ስሰክር ስለ ሁለቱም ጉበቶቼ ደንታ ስለማይሰጠኝ፣ በራሴው እጅ የራሴው ጤና ላይ አልኮል እለቅበታለሁ፣ በራሴው እጅ ራሴው ጆሮ ላይ ደሞ  ጩኸት፡፡ መጠጥን እንደምጠላው ላፕቶፔን መጥላቴ ምክንያቱ ከዚህ ግንኙነት የመነጨ ሳይሆን አይቀርም፡፡
መጠጡ እና ሙዚቃው በሂደት እንደሰባበሩኝ፣ እኔም በሂደት የመጠጥ ጠርሙሱን እና ላፕቶፑን ሰበርኳቸው፡፡ በላፕቶፑ ጠርሙሱን ወይንም በጠርሙሱ ላፕቶፑን የትኛውን ለየትኛው መስበሪያ እንደተጠቀምኩ አላውቅም፡፡ ድምጽ በሚያወጣው ላፕቶፕ እብደት የሚያወጣውን ጠርሙስ ወይንስ ተገላቢጦሽ?
ብቻ ጠዋት ስነቃ…ሦስታችንም ተሰባብረን ወድቀናል፡፡ ከፍተኛ ጩኸት የጆሮዬን ጉበት፣ ከፍተኛ መጠጥ የሆድ እቃዬን ጉበት ከጥቅም ውጭ አድርገውታል፡፡ ከውስጥ እቃዎቼ ውጭ የሚላወስ እኔነት ካለኝ እሱም ገንዘቤን የማገኝበት ስራዬ ነበር። ስራዬንም በራሴ እጅ ቆርጬ ጥየዋለሁ፡፡ ስራዬ በሙሉ ያለው ላፕቶፔ ላይ ነው፡፡ ላፕቶፕ ከሌለ ስራ የለም፡፡ በራሴ እጅ ራሴን እንደ ዳማ እየዘለልኩ በልቼ ጨርሻለሁ፡፡ ራሴን በልቼ በውድቀቴ ላይ ነግሻለሁ፡፡ ስለዚህ ስራ ለተወሰነ ጊዜ አቆምኩ፡፡
ስራ ሳቆም ገንዘብ ቆመ …ገንዘብ ሲቆም አልኮል መጠጣት ቀረ፡፡ ገንዘብ ሲቆም ወደ ከተማ መውጣት ቀረ፡፡ ወደ ከተማ መውጣት ሲቆም ጩኸት ቀረ፡፡ ጩኸት ሲቀር የተደበቀችው ነፍሴ ቀስ እያለች ወደ ጆሮዬ ብቅ ማለት ጀመረች፡፡
እንዲህ ከተሸሸገችበት ወደ ጆሮ አፋፍ ወጥታ ብቅ በማለት ላይ ሳለች አንድ አጋጣሚ መጣ፡፡ እጄን መልሶ የሚሰጠኝ አጋጣሚ፡፡ እጅ የሚሰጠኝ አጋጣሚ ጩኸትን መልሶ የሚሰጠኝ አጋጣሚም መሆኑ አልጠፋኝም፡፡ ላፕቶፔ ሲጠገን ነፍሴ እንደሚበላሽ፣ ላፕቶፔ ሲጠገን ኪሴ እንደሚሞላ እና ሰላሜ እንደሚጐድል አውቀዋለሁ፡፡ ግን ጉድለቴ ናፈቀኝ። ነፍሴም ሰብቶ አስጨነቀኝ፡፡ ገዳም ሊያስገባኝ ሆነ። ‘ኦሽ’ን ሊያደርገኝ ያስፈራራኝ ጀመር። ላፕቶፑ ተጠገነ፡፡
ጉበቱ ባለቀ ጆሮዬ ውስጥ በቀስታ የመጀመሪያውን ሙዚቃ ከፈትኩ፡፡ ነፍሴ ሰብቷል፡፡ የሚያርፍበት ነገር ያስፈልገዋል፡፡ በአይን የሚገባውን ንባብ፣ ከአፍ የማያልፈውን ፀጥታ ለወራት አጣጥሟል፡፡ ነፍሴ በጆሮዬ በኩል ብቻ ተርባለች፡፡
ሰባራው ላፕቶፕ ሲጠገን… እንደኔው ረጋ ያለ ሆኗል፡፡ ፍጥን - ፍጥን አይልም፡፡ ክፈት ሲባል ብዙ ያስባል፤ ያሰላስላል፡፡ “መክፈት ጥሩ ነው አይደለም?” ዝጋ ሲባልም ያስባል “መዝጋት ጥሩ ነው አይደለም?”
እኔ እና ላፕቶፔ አንዳችን ሌላችንን ሰብረን፣ እርስ በራሳችንን ተሰባብረን፣ እርስ በራሳችን ተጠጋግነን ተመልሰን አንድ ቤት ገብተናል፡፡ ሁለታችንም ረጋ ያልን ሆነናል፡፡ ላፕቶፑ ከዚህ በፊት እንደ እቃ ነበር። የእቃ ስም ነው የነበረው፡፡ የጅምላ ስም የጅምላ ጠባይ፡፡ አሁን ግን መንፈስ አበቀለ፡፡ የሰው ባህርይ አወጣ፡፡ ዝግ አለ፡፡ አርቆ አስተዋይ ሆነ፡፡ እቃን አሰላሳይ የሚያደርገው “ቫይረስ ሲጠቃ ነው” የሚሉትን አላመንኳቸውም፡፡
“HP” የሚል የእቃ ስሙን ቀይሬ “ገብሬ” ብዬ ክርስትና አነሳሁት፡፡ “ገብረ - እኔ” ነው። በውስጡ ያመቃቸውን ሙዚቃዎች አስመርጦ አንዲቱን በዝግታ ከፈተልኝ፡፡
የፒያኖ ሙዚቃ ነው። ያዘነ ሙዚቃ። ባዘነ ሙዚቃ አንደበት የሚተረክ፡፡ ተሰብረው የተጠገኑ ጣቶች የሚወለውሉት ሙዚቃ። ጣቶቹ ፒያኖውን በደንብ ያውቁታል፡፡ ማለት የፈለጉትን ያናግሩታል። በል ተብሎ የታዘዘውን ብቻ ሳይሆን ማለት የፈለገውንም ነው ማዜም የሚችለው። ላፕቶፔ የፒያኖውን እና የተጫዋቹን ሀዘን ቀስሞ አስደመጠኝ። ነብሴ አደመጠች፡፡ አድምጣ ተነካች። ለካ ለማድመጥ ማዘን ያስፈልጋል፡፡ ድሮ፤ የሬሳ መሸኛ ይመስለኝ የነበረው የክላሲካል ሙዚቃ፣ በአዲስ መንፈስ ራሴን እንድቀበል አደረገኝ፡፡ የተሸኘው ሬሳ የበፊቱ ቅብጥብጥነቴ ነበር፡፡ የበፊቱ ቅብጥብጥነቴ ከቅብጥብጡ አዲስ ኮምፒውተር ጋር ተሸኝቷል፡፡ አዲሱ እርጋታዬ ረጋ ካለው ላፕቶፕ ጋር ተወልዷል።
ላፕቶፑ የፒያኖውን ሙዚቃ ቀድቶ አይደለም የሚያስደምጠኝ፡፡ የተሰበረ አራዳ ማለት ራሱ ለካ ፒያኖ ነው፡፡ ሰባራ እቃዎች እና ሰባራ ሰዎች ለካ አንድ ናቸው፡፡ ሰው እና መኪና፣ ባርያና ጌታ አይደሉም ለካ፡፡ መኪናውን የሰራው ሰው ቢሆንም ሰው እና መኪና አንድ ላይ ሆነው ነው የሚነግዱት፡፡ ሰው እየነዳ አጋጨው ቢባል ወይንም መኪናው እየተነዳ ተጋጭ ቢባልም እንኳን፣ አደጋው ግን አንድ ላይ ነው የሚደርስባቸው፡፡ ከአደጋው በኋላ ይግባባሉ፡፡ መኪናውም ጋራዥ ሰውም ሆስፒታል ይገባል፤ አንድ ላይ በተጓዙበት የቅብጥብጥነት መዘዝ፡፡
ከላፕቶፑ ውስጥ የወጣው የሚያሳዝን ሙዚቃ፤ የሰው ብቻ ሳይሆን የእቃዎችም እሮሮ ነው፡፡ አንድ ላይ ነው የሚወድቁት፡፡ ሙዚቃውን የሚሰማው የደረሰው ሰው ብቻ አይደለም፡፡ እኔም እሰማዋለሁ። መስማት የቻልኩት ግን አሁን ነው፡፡ ሙዚቃውን የደረሰው ሰውን አይነት ሀዘን ሲደርስብኝ፡፡ ፒያኖው ከእንጨት ቢሰራም ሀዘንን የመግለፅ አቅም ስላለው ነው ሙዚቃውን ለማፍለቅ ያስቻለው፡፡ የመግለፅ አቅም ደግሞ የመረዳትም አቅም ነው፡፡
ላፕቶፔ ተሰብሮ ባይጠገን… ተሰብሮ የተጠገነ ፒያኖን ለቅሶ ማስተጋባት ባልቻለ ነበር፡፡ እኔም ተመሳሳይ ነኝ፡፡ ተጐድቼ ባልድን፣ ጐድቼ የማዳንን ጣዕም ባላወቅሁ ነበር፡፡ የሙዚቃ ትርጉም ራሱ በአጭሩ መጐዳት እና መዳን ነው፡፡ የጥበብ የመጀመሪያ ልሳን ሙዚቃ ነው፡፡ ሙዚቃን ለማድበስበስ ንግግር ሙዚቃን እየቆራረጠ፣ እየተንተባተበ ይገባል። መንተባተቡ የማያስታውቅ በውበት የተቀመመ ንግግር “ግጥም” ተብሎ ይጠራል፡፡
በመጥረቢያ ከተፈለጠ ዛፍ ውስጥ የሀዘኑ ቅርጽ የሚገለጥበት መንገድ ከተቸረው… ፒያኖ ሆኖ ስሜቱን ይገልፃል፡፡ ዛፉ…ዛፍነቱን በመጥረቢያ ስለት ሲያጣ ያዝናል፤ በአናጢ ህክምና ከሞተው ዛፍነቱ እና ሀዘኑ ተላቅቆ ፒያኖ ሆኖ ይወለዳል፡፡ ሳይወለዱ መሞትም ሆነ ሳይሞቱ መወለድ አይቻልምና፡፡
የአፈጣጠር ሞቱን ከአወላለዱ ጋር… ስቃዩን ከደስታው ጋር እየመዘነ ፒያኖው ያዜማል፡፡ ሰው ባይቆርጠው እንጨቱ አያዝንም…ሰው ፒያኖ አድርጐ ባይወልደው እንጨቱ አይዘፍንም፡፡
ሰውንም እንደ ዛፉ የሚቆርጠው ሀዘን ይገጥመዋል፡፡ ከሀዘኑ ሲያገግም ስንኝ ወይ የሙዚቃ ዜማ በውስጡ ያበቅላል፡፡ በውስጡ የበቀለውን ሀዘን ወደ ውልደት የሚቀይረው በመሳሪያዎች አማካኝነት ነው፡፡
እነዚያም መሳሪያዎች ግን እንደሱው ከድሮው ማንነታቸው ተቆርጠው በአዲስ ማንነት የበቀሉ እስካልሆኑ ድረስ በውስጣቸው መልዕክትን ማስተላለፍ አይችሉም፡፡ የሚያስተላልፉት መልዕክት የሰው ልጆችን የስጋ እና ደም እንጉርጉሮ ብቻ ሳይሆን… የራሳቸውንም የቁስ ነብስ እሮሮንም ጭምር ነው፡፡ ስለሚሆንም፤ ተሰብረው የተቃኑ የእቃ እና የሰው ነፍሶች በትብብር አዲስ ውበት ይፈጥራሉ፡፡
ቀርከሃ ጐብጦ ወንበር ይሆናል፤ ሰው ጐብጦ ይቀመጥበታል፡፡ አንዱ በመቀመጥ ሌላው በማስቀመጥ አዲስ ማንነታቸውን ያሳርፋሉ፡፡ ባልተቆረጠ እና በጋለ ሚስማር ባልተበሳ ሸንበቆ ዜማ አይወጣም፡፡ ሸንበቆውን የሚቆርጠው እና የሚበሳው ሰው መሳሪያውን ማበጀት የቻለው… ከራሱ ህይወት ውጣውረድ… የተቆረጠውን እና አለፍ አለፍ ብሎ በጊዜ እና እጣ-ፈንታ የጋለ ሚስማር የተበሳበትን ልምዱን በሸንበቆው ላይ ተርጉሞ ነው። በሸንበቆው ቀዳዳ የሚልከው እስትንፋሱ ከእኩል የህልውና ክፍተቱ እና የሀዘን ሽንቁሮቹ ጋር የተስማማ እስካልሆነ ድረስ ውበት አይደመጥም፡፡
ሙዚቃው በላፕቶፔ አንደበት ሲያንጐራጉር ከላይ ሹክ አለኝ፡፡ ወይንም ያለኝ መሰለኝ፡፡ ሙዚቃውን ደጋግሜ አደመጥኩት፡፡ መልዕክቱ አንድ ነው፡፡ ነፍሴ በጆሮዬ ወጥታ በሙዚቃው ውበት ላይ ትርጉሟን አገኘች፡፡ ባገኘችው ትርጉም ላይ በፀጥታ አርፋበት ቆየች፡፡ በፀጥታው ውስጥ እኔነቴን በሁሉም ነገር ላይ አንድ ሆኖ አገኘሁት፡፡
አልጋዬም፣ ወንበሬም፣ መስታወቴም እኔን ስለመሆናቸው እርግጠኛ ሆንኩኝ፡፡ አሁን በመኖሪያ ቤቴ ውስጥ እኔን መስለው የከበቡኝ እቃዎች ሁሉ…በሀዘን ውስጥ አደብ ገዝተው በፀጥታ የተዋጡ… ተሰብረው የተጠገኑ የስጋ ዘመዶቼ መሆናቸው ታወቀኝ፡፡  

Published in ህብረተሰብ

(ለቅላቂዎችና አስለቅላቂዎች)

    የቀድሞውም ሆነ የአሁኑ የእንድማጣ ኢየሱስ ት/ቤት የሚገኘው በደብረ ማርቆስ ከተማ ምሥራቃዊ ክፍል የአሁኑ የደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ካለበት አካባቢ ነው፡፡ ት/ቤቱ የተመሰረተው ለጥ ብሎ ከሚታየውና ሣር በበዛበት የውሰታ ወንዝ ሜዳ ላይ ነው፡፡ የውስታ ወንዝ ከላይ ከደጋው እየወረደ መስኩን ለሁለት ሰንጥቆ የሚጓዝ አነስተኛ ወንዝ ነው፡፡
ዋለልኝ አዘነ የተባለ ዘፋኝ እንዲህ ሲል ውሰታን ያነሳሳዋል፡-
ደገኛ በቆሎውን ይለዋል አምባላይ፣
ቤቷ ደብረ ማርቆስ ከውሰታ በላይ፡፡
ድምፃዊው ሙሉቀን መለሰ ደግሞ
እንድማጣ ማርያም እጥጓ ደርሼ
ወይ አለመታደል መጣሁ ተመልሼ
ብሎ ዘፍኗል፡፡ ነገር ግን እንድማጣ ኢየሱስ እንጂ እንድማጣ ማርያም የምትባል ቤተክርስቲያን በአካባቢው የለችም፤ አልተሰራችም፡፡ ይልቅ በዋናው በደብረ ማርቆስ ከተማ አከማ ማርያም የተባለች ታሪካዊት ቤተ ክርስቲያን ትገኛለች፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ የጥንት ገዥዋ ደጃች ተድላ ጓራ በዐረፉበት ወቅት
የውሽ ወስደው  ጣሉት ደጃዝማች ተድላን፡፡
ይነሳ ነበር አከማ ቢሆን
ተብሎለታል፡፡ ይኸውም ደጃች ተድላ ጓሉ መቀበር የነበረበት የውሽ ሚካኤል ሳይሆን አከማ ማርያም ነበር ለማለት ነው፡፡ ምስጢሩም አከማ ቢሆን ኖሮ ይነሣ ይታወስ ነበር ለማለት ነው፡፡
እንድማጣ ኢየሱስ የት/ቤቱን ዳገታማ ቦታ አልፎ ከሜዳው ላይ ይገኛል፡፡ ከዳገቱ ሥር ደግሞ የአንደኛ ደረጃው ትምህርት ቤት ይገኛል፡፡ ት/ቤቱ የተመሰረተው ረግረጋማና ለምለም ሳር በበዛበት ቦታ ላይ ነበር፡፡ በቦታው ረግረጋማነት ት/ቤቱ እየሰመጠ ስለአስቸገረ፣ ዛሬ በአጭር ርቀት ከደረቁና ከዳገታማው ሥር ተገንብቶ አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡
በ1961 ዓ.ም አሀዱ ብዬ ትምህርት ቤት የገባሁት 3ኛ A ነው፡፡ በወቅቱ የስም ጠሪ መምህራችን ወ/ት ሙሉቀን ታደሰ ትባል ነበር፡፡ የሞጣ ሰው እንደሆነች አልፎ አልፎ ስታወራ እሰማ ነበር፡፡ በጊዜው ት/ቤቱ የተደራጀው ከአምስተኛ እስከ 6ኛ ክፍል ሲሆን ያኔ የ6ኛ ክፍል ተማሪዎች የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ያህል ነበር የሚታዩት፡፡
ሦስተኛ ክፍል ገብቼ ለመማር የምችል መሆኔን የሚገልጽ ሰርተፊኬት የሰጡኝ አቶ ሸዋቀና ዘውዴ የተባሉና በጊዜው የጎልማሶችና ማይማን ኃላፊ የነበሩ ሰው ናቸው፡፡ በወቅቱም፡
ትምህርት ተስፋፋ ከፍ ከፍ ባለ ዘዴ፣
በዳሬክተራችን ሸዋቀና ዘውዴ
እየተባለ ደብረ ማርቆስ ውስጥ ይወደሱ ነበር። እንድማጣ ኢየሱስ የተባለው አዲሱ ትምህርት ቤት ተማሪዎችን እየተቀበለ እስከ ስድስተኛ ክፍል ያስተምራል መባልን እንደሰማሁ አቶ ሸዋቀና ዘውዴ የሰጡኝን ሰርተፊኬት ይዤ ወደ ት/ቤቱ ሄድኩ፡፡ የት/ቤቱ ርዕሰ መምህር አጭርና ጠይም መልክ ያላቸው አቶ ጋሻው ከበደ ነበሩ፡፡ በጠባያቸው ኮስተር ረጋ ያሉ አስተዋይ ሰው ናቸው፡፡ ሁኔታዬን አይተውና ገምግመው ለ3ኛ ኤ ስም ጠሪዋ ለወ/ት ሙሉቀን ታደሰ ማስታወሻ ጽፈው፣ የይግባ ፍቃድ ፈርመው ሰጡኝ፡፡
ወደ ት/ቤቱ የሄድኩት ጋቢ ለብሼ ስለነበር፣ “ከነገ ጀምሮ ጋቢ ለብሰህ እንዳትመጣ” በማለትም አስጠነቀቁኝ፡፡ በነጋታው በእድሜ ከእኔ ከሚያንሱ ልጆች ጋር መስመር መስመር ይዞ ከተዘጋጀው ግንዲላ ላይ ስቀመጥ ሁሉም አትኩረው አዩኝ። ያኔ በክፍል ውስጥ ልጆቹ የሚማሩት በተጠረበ ግንዲላ ላይ በመቀመጥ ነበር፡፡ ከ1ኛ እስከ ስድስተኛ ያሉት ክፍሎች ሊሾ ስላልተደረጉ በየሳምንቱ ዐርብ ዐርብ በክፍል አለቆች አማካይነት እበት ከየቤቱ እየመጣና ከሜዳም እየተለቀመ ክፍሎች ሁሉ የጤፍ አውድማ እስኪመስሉ ድረስ ይለቀለቁ ነበር፡፡ በየቀኑ በመውጫ ሰዓት ላይ በተመደበው ተረኛ ይጠረጉና ይጸዱም ነበር፡፡ አስለቅላቂዎችና አስጠራጊዎች የየክፍሉ አለቆች ሲሆኑ ለቅላቂዎችና ጠራጊዎች ደግሞ ተማሪዎች ናቸው፡፡
እኔ 3ኛ ክፍል ስገባ፣ የክፍል አለቃው በፈቃዱ ለሽተው ይላል ነበር፡፡ በክፍሉ ቁጥር አንድ ረባሽ ደግሞ አቤ ኅብስት ይባላል፡፡ አቤ ኅብስት ፊቱ ሾል፣ ዓይኑ ደቀቅ ያለ ቁመተ ረጅም ተማሪ ነበረ። ከሁሉም ተማሪ ጋር በመጣላትም ይታወቃል። ሁልጊዜ ይከሰሳል ይከስሳል፡፡ በፍቃዱ ለሽተው ደግሞ ገራገርና ቅንም ስለሆነ ሳይቀጣ ያልፈዋል። በዚህ ድርጊቱ በፈቃዱ ለሽተው ተሽሮ እኔ አለቃ ሆንኩ፡፡፡
አቤ ኀብስት በየቀኑ መረበሽና መክሰስ ይወድዳልና እኔን በክፍሉ የስም ጠሪዋ በወ/ት ሙሉቀን ታደሰ ዘንድ ከሰሰኝ፡፡ እርስዋ ፊት እንደቀረብኩ፤ “ዐቃጣሪ” ብዬ ሰደብኩት፡፡ ለካንስ እንዲህ ተብሎ አይሰደብም ኖርዋል፡፡ እትየ ሙሉቀን ቱግ አለችና ጣቶቼ ደም እስኪያንጠባጥቡ ድረስ ገረፈችኝ፡፡ እኔም በተራዬ የክፍል አስለቅላቂ ሆኜ ስሰራ፣ አቤ ኅብስት ሳይለቀልቅ በመቅረቱ አስገርፌዋለሁ፡፡ ከ1ኛ እስከ 6ኛ ላሉ ክፍሎች ዋናው የተማሪዎች ተጠሪና አስለቅላቂ ደግሞ ሙሉነህ ሰውነቴ የሚባል ተማሪ ነበር፡፡ በተለይ መምህራን ቀብር ሲሄዱ በየክፍሉ እየገባ ት/ቤቱን ይቆጣጠር ነበር፡፡ ሙሉነህ ረጅም፣ ቀጭንና ጠባዩ የተመሰገነ ልጅ ሲሆን ልክ እንደኛ ሁሉ ቁምጣውን ለብሶ በባዶ እግሩ ነበር የሚጓዘው። ሰውነቱ ቀጭን ስለሆነ ቁምጣው ከአሁን አሁን ሾልካ መሬት ላይ የምትወድቅ ትመስል ነበር፡፡
አንድ ጊዜ ደሞ ለት/ቤቱ ማስፋፊያ ገንዘብ ይዋጣ ተብሎ የሀብታም ቤተሰብ ብር 150፣ መኸከለኛ 100፣ በጣም ዝቅተኛ 50፣ ከዚህ ያነሰው ብር 30 እንዲከፍል በወላጆች ኮሚቴ ጭምር ተወሰነ፡፡ እና እኔም በጊዜው ብር 50 እንድከፍል ተጠይቄ ነበር። ነገር ግን ደብረ ማርቆስ ምንም ዓይነት ቤተሰብ እንደሌለኝ ለወላጆች ኮሚቴ ሊቀመንበር ለአቶ ይኩኖ ነግሬ በነጻ እንድማር ፈቅደውልኝ መማሬን ቀጠልኩ፡፡
በወቅቱ ከነበሩ መምህራን ውስጥ አቶ ሙሉቀን፣ አቶ ዘለቀ፣ ወ/ት ሙሉቀን ታደሰ (ብቻ በጊዜው በት/ቤቱ ውስጥ ወንድም ሴትም ሆነው 3 ሙሉቀኖች ነበሩ) እንደገና የመዝሙር መምህራችን ጋሽ ጫኔ አይረሱኝም፡፡ ከላይ እንደገለፅኩት ት/ቤቱ የተሰራው ሳር በበዛበት ቀዝቃዛ ቦታ ላይ ስለነበር ጧት ጧት ብርዱ ሲያንቀጠቅጥ ለጉድ ነው፡፡ ትንሽ ያረፈደ ተማሪ ደግሞ (መቼም የዘበኛ ደግ የለውምና) ኃይለኛና ጨካኝ በነበሩት በአባ ደምሴ፣ እጅና እግሩ ይገረፋል፡፡ እያለቀሰ ወደ ክፍል የሚገባው ተማሪ ብዙ ነበር፡፡ ተማሪ ሁሉ ደስ ይለው የነበረው ረፋዱ ላይ በመዝሙር ክፍለ ጊዜ ወደ ውጭ ሲወጣ ነው፡፡ በት/ቤቱ ሳር ላይ በባዶ እግር እየተሯሯጡ መጫወት በጣም ያስደስት ነበር፡፡
የመዝሙር አስተማሪው ጋሽ ጫኔ አጠር ያለና ቀይ ሲሆን ሁልጊዜ በኮትና ሱሪው ላይ ነጭ ጋቢ ደርቦ ይመጣል፡፡ መስኩ ላይ ያስቀምጠንና መዝሙር አስመርጦን ዘምሩ ይለናል፡፡ መዝሙሩን ሞቅ አርገን መዘመር ስንጀምር፣ “እንዳታቋርጡ መጣሁ” ይለንና በእንጨት አጥሩ በኩል ሾልኮ ወደ አንዱ አረቄ ቤት ይገባል፡፡
እኛም መዝሙሮችን እያማረጥን እያጨበጨብን እንዘምራለን፡፡ እኔም ከአስለቅላቂነቴ በተጨማሪ አዘማሪ ነበርኩ፡፡ ያኔ ጋሽ ጫኔ ከሚያስዘምረን መዝሙሮች ውስጥ ትዝ የሚለኝ፡-
“ሰንደቅ ዓላማችን ስንላት በዜማ፣
ግሩም ያላት ግርማ ግሩም ያላት ግርማ፡፡”
“ለባላገሮች ቤት አላቸው፣
ይደሰታሉ በአዝመራቸው፡፡”
“ደስ ይበልሽ ጎጃም
ፍኖተ ሰላም፡፡”
“መንግሥት እንደ ዳዊት ቡራኬ
እንደ ሴም፣
አንዲት የተሰጠው ማንም ሰው የለም፡፡”
“ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ፣
መልካም ባለሙያ፡፡”
ከመዝሙር መዝሙር እያማረጥን ስንዘምር ጋሽ ጫኔ ሙክክ ብሎ፣ ዓይኑ በርበሬ መስሎና አንደበቱ ተኮላትፎ ይመጣል፡፡ ከዚያም ወደ ክፍላችን እንድንገባም ያባርረናል፡፡ ቀድሞ የእንድማጣ ኢየሱስ 1ኛ ደረጃ ት/ቤት የነበረበት ቦታ በረግረጋማነቱ ምክንያት ፈርሶና ሜዳ ሆኖ ሳየው የቆየ ትዝታ ቀስቀሶብኝ ነው ይህችን ጽሑፍ የተከተብኳት፡፡ ቦታው እድለኛ ሆኖ ከበላዩ ዩኒቨርሲቲ መከፈቱም በእጅጉ ያስደስታል፡፡ እሰየሁ ብያለሁ!!

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 28 March 2015 09:07

‘ተጨማሪ አርባ ከመቶ’

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሰውየው ጓደኛውን…
“እስቲ የወር ገቢህን ለምን፣ ለምን እንደምታውለው ንገረኝ…” ይለዋል፡፡ ጓደኝየውም ያብራራለት ገባ…
“ሠላሳ ከመቶ ለቤት ኪራይ፣ ሠላሳ ከመቶ ለልብስ፣ አርባ ከመቶ ለምግብ፣ አርባ ከመቶ ደግሞ ለመዝናኛ፣” ይለዋል፡፡
ሰውየው ሂሳቡን ሲያሰላ የጓደኛው ወጪ ከሚያገኘው የወር ገቢ ይበልጥበታል፡፡ “አሁን የነገርከኝ እኮ መቶ አርባ ከመቶ ነው የሚመጣው…” ይለዋል፡፡ ጓደኝየውም ምን አለ መሰላችሁ…
“ይኸውልህ ዘንድሮ ኑሯችን ገቢ መቶ ከመቶ፣ ወጪ መቶ አርባ ከመቶ ሆኗል፣” ብሎት አረፈ፡፡
እናማ… እንደ አያያዛችን ከሆነ ‘መቶ አርባ ከመቶ’ ወጪንም “እሱማ ተገኝቶ ነው!” የምንልበት ጊዜ ሊመጣ ይችላል፡፡ አብዛኞቹ ነገሮች (በተለይ የምግብ ሸቀጦች) በየሳምንቱና ሲብስበትም በየሁለትና ሦስት ቀኑ የሚጨምርባት አገር ብትኖር የእኛዋ ብቻ ሳትሆን አትቀርም!
የደላቸው አገሮችማ ‘ኮንሲዩመር ፕሮቴክሽን’ ምናምን የሚባሉ መብቶቻቸውን የሚያስከብሩላቸው ህጎችና ቡድኖች አሏቸው። ሲብስና ዋጋ እየጨመሩ የሚያስቸግሩ ካሉ…አለ አይደል… “በቃ፣ አንገዛም፡፡ ምን ምን እንደምትሆኑ እናያለን…” ብለው መደብሮቹን የዝንብ መፈንጫ ያደርጓቸዋል፡፡ እኛ ዘንድ ግን የሆነ ነገር ዋጋ በጨመረ ቁጥር… “ነገ ደግሞ እንዳይጨምሩ ቶሎ እንግዛ…” ተብሎ ግፊያ ነው፡፡ ከዛም በየድራፍቱ ላይ… “በረሀብ ሊገድሉን ነው…” እያልን ማማረር ነው፡፡
የምር ግን…ነገሬ ብላችሁ እዩማ…በዚህ ወር ለምግብ ሸቀጦች የምታወጡት ወጪ ከመጪው ወር ጋር እኩል ከሆነ… አለ አይደል…‘ታስበው የሚውሉና የሚያድሩ’ ምሳና እራቶች አሉ ማለት ነው፡፡
እናማ… ‘ተጨማሪዋን አርባ ከመቶ’ ያለወለድ በማበደር ‘ታሪክ የሚያስመዘግብ’ ባንክ ይፈጠርልንማ!
ከ‘ተጨማሪ አርባ ከመቶ’ የምንድንበት ጊዜ ይምጣልንማ!
(የኮንዶሚኒየም ዕድለኞች እንኳን ደስ አላችሁ! ‘የዋጋ ማስተካከያው’ እንዴት ነው… ነገርዬው ‘ተጨማሪ አርባ ከመቶ’ አይነት እንዳይሆን ብዬ ነው፡፡ ቢሆንም ይሁን… ልጄ፣ “ምነው ሰጥተውኝ የፈለገውን ክፈል ቢሉኝ…” የሚል ስንትና ስንት ሺህ ህዝብ አለ!)
ከ‘ተጨማሪ አርባ ከመቶ’ የምንድንበት ጊዜ ይምጣልንማ!
ስሙኝማ…የሆነ ነገር ትዝ አለኝማ…ተመሳስለው የተሠሩ ነገሮች አልበዙባችሁም!“….ምርቶቻንን አስመስለው የሚሠሩ እንዳሉ ስለደረስንበት…” ምናምን የሚሉ ነገሮች እየተለመዱ ነው፡፡ እናማ… ግራ የሚገባን… አለ አይደል…ይሄ ሁሉ ‘አስመስሎ ሠሪ’ እያለ እንዴት ነው የሆነ ‘ጋማውን የሚያዝ’ የሌለው! ልክ ነዋ…“እከሌ ድርጅት የእከሌን ድርጅት ምርት አስመስሎ መሥራቱ ስለተረጋገጠበት…” የሚል ነገር የማንሰማሳ! አሀ…አንዳንድ ጊዜ “ይቺ እንኳን የፕሮሞሽን ‘ፊንታ’ ነች…” የሚል ጥርጣሬ ሊያድርብን ይችላላ!
ለነገሩ ምን መሰላችሁ… “ያልጠረጠረ ተመነጠረ” የምትለው ተረት ዘመኗ ነው፡፡ ልክ ነዋ…ብዙ ነገሮችን ተመሳሰለው የተሠሩ ይሁኑ ‘እውነተኛዎቹ’ ለመለየት እየተቸገርን ነዋ!
ለነገሩማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል… የተለያዩ ምርቶች ብቻ ሳይሆኑ ‘ተመሳስለን የተሠራን’ ሰዎችም ቁጥራችን ቀላል አይደለም፡፡ በአለባበስ በሉት፣ በአነጋገር በሉት፣ በአረማመድ በሉት፣ በቢራ አጨላለጥ በሉት፣ …ምን አለፋችሁ በየፊልሙ በየምናምኑ ላይ ካየነው ጋር ‘ተመሳስለን የተሠራን’ ለመምሰል የምንሞክር መአት ነን፡፡
ታዲያላችሁ…በቀደም አንድ መዝናኛ ቦታ የሆኑ ወጣት ሴቶች የ‘ታቱ’ ዋጋ በጣም እየጨመረ መሆኑን እየተናገሩ ሲበሳጩ ነበር፡፡ ‘ተጨማሪ አርባ ከመቶ’ አይነት ነገር በሉት፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል… ‘ታቱ’ እየተለመደ አይደል! በነገራችን ላይ የሆነ ግርም የሚለኝ ነገር አለ… ‘ንቅሳት’ የሚለውን ቃለ ላለመጠቀም “ታቱ እንሠራለን…” ከተማችን በተለያየ ቦታ ታያላችሁ፡፡ የምር እንነጋገር ከተባለ… “ታቱ እንሠራለን…” ከሚለውና “ንቅሳት እንነቅሳለን…” ከሚለው አሪፉ የቱ ነው! ምን ይደረግ… ‘በእንግሊዝኛ የማነጠስ’ አይነት ‘ተመሳስሎ የመሠራት’ አባዜ ስላለብን አልለቀን ሲልስ! እናላችሁ… ድሮ ‘ኒቂሴ’፣ ‘አዲስ ዘመን ጋዜጣ’ ምናምን እየተባለ ይቀለድባት የነበረችው ንቅሳት ዞራ ‘ታቱ’ ተብላ ስትመጣ እኛ ቀለብናታ!  ምናልባት ነገርየው ያልገባን ካለን… ‘ታቱ’ ማለት ‘ንቅሳት’ ማለት ነው፡፡ (‘አራት ነጥብ!’ የሚለውን ጨምሩልኝማ!)
ከ‘ተጨማሪ አርባ ከመቶ’ የምንድንበት ጊዜ ይምጣልንማ!
ይሄን ሰሞን በማህበራዊ ድረ ገጾች ላይ የሚቀባበሏት ነገር አለች… የተለቀቀብን ‘ስሪ ጂ ነው፣ ስሪ ጅብ’ የምትል፡ የምር እኮ…‘ሙልጭ የማድረግ’ አይነት አለው እንዴ! እኔ ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…በተለይ በዚህ ዘመን ብዙ ነገር ከኢንተርኔት ጋር የተያያዘ እየሆነ መጥቷል፡፡ ስለመጣ ሁላችንም ሳንሳቀቅ የምንጠቀምበት ‘ዋጋ’ ቢኖር አሪፍ ነው፡፡ ይኸው ባንኮቹ ሁሉ… አለ አይደል… ‘እኛ ዘንድ በመመላለስ እግራችሁ ሳይቀጥን ባላችሁበት ሆናችሁ ሁሉንም ነገር በኢንተርኔት መጠቀም ትችላላችሁ…’ አይነት ነገር እያሉን አይደል!
የምር ግን…ነገ፣ ተነገ ወዲያ ደግሞ እንደ ሌሎቹ ሀገራት እቤታችን ቁጭ ብለን ለመገበያየት፣ ታክስ ለመክፈል፣ …ምናምን እንዲያበቃን ከአሁኑ የሚያስፈሩን ነገሮች ባይኖሩ አሪፍ ነው፡፡ በዚሀ ላይ ደግሞ በኢንተርኔት አጠቃቀም በዓለም ያለንበትን ደረጃ እናውቀዋለን! ኢንተርኔት የመሳሰሉ አገልግሎቶች ‘እንደ ቦኖ ውሀ’ ለሁላችን የሚደርስበትን ዘመን ያምጣልንማ!
ከ‘ተጨማሪ አርባ ከመቶ’ የምንድንበት ጊዜ ይምጣልንማ!
እኔ የምለው…ስልክ ምናምን ሰፈር ከደረስን አይቀር… የአገልግሎት ጥራት ይሻሻልንማ! ልክ ነዋ…ጥሪያችን መሀል ላይ እየተቋረጠ…“እንዴት ጆሮዬ ላይ ትዘጋለህ!…” ምናምን አይነት ጠብ ያመጠብናላ!
እግረ መንገዴን ይቺን ስሙኝማ…ሰውየው ሌሊት የተሳሳቱ ጥሪዎች እየረበሹት ተቸግሯል፡፡ ለቴሌፎን ኩባንያው አቤት ቢልም ምንም መፍትሄ ሊሰጡት አልቻሉም፡፡ ታዲያላችሁ…አንድ ቀን ከሌሊቱ ስምንት ሰዓት ላይ የሆነ ቁጥር ላይ ይደውላል። ስልኩም ይነሳል፡፡ ከወዲያኛው ጫፍ  እንቅልፍ ያንጎላጀጀው ድምጽ “ሄሎ ማን ልበል?” ይላል፡፡
“የቴሌፎን ኩባንያው ሥራ አስኪያጅ ነህ?”
“አዎ ነኝ፣ በዚህ ሰዓት የሚደውለው ማነው?”
“በተሳሳተ የስልክ ጥሪ ከሌሊቱ ስምንት ሰዓት መቀስቀስ ምን እንደሚመስል እንድታውቀው ብዬ ነው…” ብሎ ስልኩን ጠረቀመው፡፡
ብቻ ሆነም ቀረ በምንም ይሁን በምን ከ‘ተጨማሪ አርባ ከመቶ’ የምንድንበት ጊዜ ያምጣልንማ!
ይቺን የሆነ ቦታ ያነበብኳትን ነገር እዩልኝማ…ወጣቷ አለቃዋ ሴት ነበረች፡፡ እናላችሁ… አንድ ቀን አለቃዋ ጎኗ ሆና ስልኩ ይጠራል፡፡ ወጣቷም ታነሳና…“ሄሎ ማን በል?” ትላለች፡፡ ከዚያም ዝም ብላ ከወዲያኛው ስታዳምጥ ትቆይና፤ “ለአንቺ መሰለኝ…” ብላ ለአለቃዋ ታቀብላታለች፡፡ አለቅየዋም ቆጣ ትልና…
“ወይ ላንቺ ነው፣ ወይ ላንቺ አይደለም ይባላል እንጂ መሰለኝ ብሎ ነገር ምንድነው!” ትላለች፡፡ ወጣቷ ምን ብትል ጥሩ ነው…
“አይ ሰውየው፣ ‘አንቺ ደደብ አሁንም አለሽ’ ሲል ላንቺ መስሎኝ ነው፣” ብላት እርፍ!
ከ‘ተጨማሪ አርባ ከመቶ’ የምንድንበት ጊዜ ይምጣልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

የኦህዴድ ድንገተኛ የርችት “ተኩስ” ክፉኛ አስደነገጠኝ

ባለፈው ረቡዕ ከሌሊቱ 6 ሰዓት ገደማ የሰማሁት ከፍተኛ የተኩስ ድምፅ እንዴት ክው እንዳደረገኝ አልነገራችሁም፡፡ ስንት ሃሳብ----ወደ አዕምሮዬ መጣ መሰላችሁ? (ለአንድዬም ቴክስት ሜሴጅ አድርጌአለሁ!) ግን የምን ተኩስ ይሆን? የእርስ በእርስ የውስጥ ሽኩቻ? ወይስ አንዱ ጥርስ የነከሰብን የአሸባሪ ቡድን አዲስ አበባ ላይ መሽጎ? ብቻ ምን ልበላችሁ ---- ስጋት፣ ፍርሃት፣ ድንጋጤ፣ ተስፋ መቁረጥ፣ ድንዛዜ ወዘተ------ በቅጽበት መንፈሴንና ስሜቴን ተቆጣጠሩት፡፡ ሞባይል አንስቶ መደዋወልም እኮ የአባት ነው፡፡ ግን ማን ከድንዛዜ ያውጣኝ?
የተኩሱ ድምፅ ሲጨምር ነው ድንገት ከተቀመጥኩበት ተስፈንጥሬ መስኮቱ ጋ የደረስኩት። መስኮቱን በጠባቡ ከፈት አድርጌ ወደ ውጭ አጮለቅሁ፡፡ ድንጋጤዬ ወደ መገረም ለመቀየር ቅፅበት አልፈጀበትም፡፡  (“ሰርፕራይዝ ኤንዲንግ” ያለው አጭር ልብወለድ በሉት!) ዓይኔን ማመን አቃተኝ፡፡ ነገርየው ተኩስ አልነበረም፡፡ ፌሽታ፡፡ ልደት፡፡ ኦህዴድ ለ25ኛ ዓመቱ ያስተኮሰው ርችት!! (ለመሆኑ ርችት ስንት ገባ?)
እናላችሁ---ወደ መስቀል አደባባይ ግድም ያለው ሰማይ፣ በሚፈነዳው የርችት ህብረቀለማት ዓለሙን ሲያይ አመሸላችሁ፡፡ እኔ ግን የርችቱ አምራች ናት ብዬ የጠረጠርኳትን ቻይና በሆዴ ወቅስኳት፡፡ ምናለ የሪችትን ድምፅ ከጦር መሣሪያ ድምጽ ለየት ብታደርገው?! እንዴት---- የፌሽታና የጥይት ድምጽ እስኪያሳሳት ድረስ አንድ ይሆናል? በሌሊቱ ሰማይ ላይ የቀለማት ምትሃት የሚሰራ የሚመስለውን የሪችት ተኩስ ጥቂት ከተመለከትኩ በኋላ መስኮቴን ዘጋሁ፡፡ ወደ መቀመጫዬ ስመለስ የደርግ 10ኛ ዓመት የአብዮት በዓል ትዝ አለኝ፡፡ (አቤት የርችት መዓት!)
አሁን ደግሞ በቀጥታ የምናመራው ወደ “ቀልድ ርችት” ይሆናል፡፡ እናላችሁ---የዓለም መሪዎች በሙሉ በአንድ ቀን ይሞቱና ራሳቸውን ሰማይ ቤት ያገኙታል። ምንጮች እንደሚሉት፤ሳጥናኤል እንደዚያን ዕለት ጮቤ ረግጦ አያውቅም፡፡ ከመሪዎቹ መካከል አንድም እንኳን የጸደቀ የለም፡፡ ሁሉም ምድባቸው ሲኦል እንደሆነ ተነገራቸው፡፡ (የምድርን ገነት ሲያጣጥም የኖረ ሁላ ገሃነም ወረደ!) እንዳልኳችሁ… አሟሟታቸው ድንገተኛ ስለነበር ቤተሰብና ወዳጅ ዘመድ አልተሰናበቱም፡፡ ምንም የተናዘዙት ነገርም የለም (መሪዎች እንሞታለን አይሉማ!) እናም ፕሬዚዳንቶቹ፤ ወደ አገራቸው አንድ አንድ የስልክ ጥሪ ያደርጉ ዘንድ ሰይጣንን አስፈቀዱት፡፡ ሰይጣንም ያለ አመሉ ሲበዛ ደግ ሆነላቸው፡፡ (“የዘላለም ፍሬንዶቼ ናቸው” ብሎ ይሆን?) የመጀመሪያው ደዋይ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ነበሩ፡፡ (በምድር ላይ ኃያል፣ በሰማይም ኃያል ነው!) ከዚያ የሩሲያ፣ የእንግሊዝ፣ የጀርመን፣ የፈረንሳይ ወዘተ… በየተራ ደወሉ፡፡
የአፍሪካ መሪዎች ከሲኦል ወደ ምድር ስልክ ለመደወልም ውራ ነበሩ፡፡ (እዚህም ውራ፤ እዚያም ውራ!) ሆኖም ከማናቸውም አገራት መሪዎች የበለጠ ረዥም ሰዓት ያወሩት እነሱ ናቸው፡፡ (ብዙ የቤት ጣጣ አለባቸዋ!) ሁሉም ደውሎ ሲጨርስ ሰይጣን፤ “Friends, you know there is no free lunch” አለና ከእያንዳንዳቸው ላይ የስልክ ሂሳብ መቀበል ጀመረ። (ሲኦልም ቴሌ አለ እንዴ?!) ወዲያው ከአሜሪካ፣ እስያ፣ አውስትራሊያና አውሮፓ ፕሬዚዳንቶች ላይ (ከእያንዳንዳቸው) 500 ዶላር ቆነደዳቸው። ለረዥም ሰዓት በስልክ ያወሩትን የአፍሪካ መሪዎች ግን (እያንዳንዳቸውን) 50 ዶላር ብቻ አስከፈላቸው። ይሄን የታዘቡት የቀሩት አገራት ፕሬዚዳንቶች በጣም ተናደው፤ “ክፍያው ኢ - ፍትሃዊ ነው!” በማለት ሲኦልን ቀወጡት። ሰይጣን በጋኔላዊ ጩኸቱ ሲያምባርቅባቸው ትንሽ ገታ አሉ፡፡ ከዚያም “ጋይስ…ምንድነው የምትሉት… የአፍሪካ ፕሬዚዳንቶች እኮ የአገር ውስጥ ጥሪ ነው ያደረጉት!” አለና ገላገላቸው፡፡ (ትንፍሽ ያለ አልነበረም!)
አያችሁ… ሲኦልና የአፍሪካ አህጉር የሚገኙት በአንድ ክልል ውስጥ ነው (ለዚህ ነው Local call ነው የተባለው!) በእርግጥ የአፍሪካ ሲኦልነት ለህዝቦቿ እንጂ ለአምባገነን መሪዎቿ አይደለም፡፡ (ለህዝቡ ሲኦልን ፈጥረው፤እነሱ ገነት ውስጥ ይኖራሉ!) የአፍሪካ ሲኦልነት አምባገነን መሪዎቿ እንደሚቦተልኩት፤ የኒኦሊበራሊዝም አቀንቃኞች የአህጉሪቷን ገፅታ ለማጠልሸት የሚነዙት ፕሮፓጋንዳ እንዳይመስላችሁ። አህጉሪቷ የሲኦል እኩያ ናት፡፡ በዓለም ላይ እጅግ ድሃና ኋላቀር አህጉር፡፡ በሚሊዮኖች የሚገመቱ ህዝቦቿ በጦርነትና በበሽታ አልቀዋል፡፡ ከ240 ሚ. በላይ አፍሪካውያን በተመጣጣኝ ምግብ እጥረት እየተሰቃዩ ናቸው (“ምግብማ ሞልቷል--” በሚዘፈንባት አፍሪካ!) መከራዋ ተዘርዝሮ አያልቅም፡፡ እስካሁን 17 ሚ. አፍሪካውያን በኤችአይቪ/ኤድስ ያለቁ ሲሆን ዛሬም ከ25ሚ. ህዝብ በላይ ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ነው፡፡ ከ40 በመቶ በላይ የሚሆነው አፍሪካዊ፤ ፊደል የማይቆጥር የዕውቀት ጨዋ ነው፡፡ (ከቆጠረማ አርፎ አይገዛም!)
እውነቱን ልንገራችሁ አይደል… አፍሪካ የምድር ሲኦል የሆነችብን የአያት ቅድመ አያቶች እርግማን ስላለብን አይደለም፡፡ የእግዜር ቁጣም እንዳይመስላችሁ። ተፈጥሮም እንዳልበደለችን ተዝቆ የማያልቅ የምድሪቱ ሃብት ምስክር ነው፡፡ የአፍሪካ ጠላቶች ቅኝ ገዢዎቿ አይደሉም፡፡ (ኧረ በስንት ጣዕማቸው!) ከራሷ ማህፀን ወጥተው የስልጣን ሱሰኝነት አምባገነን ያደረጋቸው የራሷ ልጆች ናቸው - ቀንደኛ ጠላቶቿ!! እስቲ ልጠይቃችሁት… አውሮፓውያን ከአፍሪካ ምድር መዘበሩ ከተባለው ሃብት ይልቅ አምባገነን መሪዎቿ የመዘበሩት አይልቅም? (የትና የት!)
ከፍተኛ የነዳጅ ምርት በማምረት ከዓለም በ4ኛ ደረጃ ላይ በምትገኘው ናይጄሪያ ---- የሆነውን አልሰማችሁም? የአገሪቱ ብሔራዊ ባንክ ገዢ፤ አንድ ማለዳ ላይ 20 ቢ. ዶላር እምጥ ይግባ ስምጥ  አይታወቅም አሉ፡፡  (መቼም “ሰላቢ” አልወሰደውም!)
ከአፍሪካ የነጭ ቅኝ ገዢዎችን ለማስወጣት የታገሉ የአህጉሪቷ የነፃነት ሃዋርያቶችን ሳስብ ግርም ይለኛል፡፡ (ማን ነበር “ነፃነት የማያውቁ ነፃ አውጭዎች” ያለው?!) እንዴ … አህጉሪቷ ነፃነቷን በተጎናፀፈች ማግስት እኮ ነው የሲኦል እኩያ የሆነችው - ዕድሜ ለአፍሪካ አምባገነኖች!! የሻዕቢያ የ30 ዓመታት የነፃነት ትግል ለኤርትራ ህዝብ ምን ፋይዳ አመጣለት? (ኢትዮጵያን እንዲጠላ ከመደረጉ ውጭ!) በእርግጥ ወዲ አፈወርቂ ላለፉት 23 ዓመታት ስልጣንን ርስታቸው አድርገው ህዝቡን ሲገዙ ቆይተዋል፡፡ (ኤርትራ ለእሳቸው ገነት፤ ለህዝቡ ሲኦል ናት!) ኤርትራውያን ዛሬ ኢሳያስ አፈወርቂ ነፃ አወጣኋት የሚሏትን አገር ጥለው እየተሰደዱ ያሉት ቅኝ ገዢ ወደተባለችው ጦቢያ ነው። ሌሎችም የአፍሪካ ህዝቦች እንደዚያው!
በነገራችን ላይ ስልጣንን የሙጥኝ ብለው ለረዥም ዓመታት ከዘለቁ የዓለማችን 20 ፕሬዚዳንቶች (Top 20) መካከል 10ሩ የሚገኙት በአፍሪካ ውስጥ ነው (እንደብርቅዬ የዱር አራዊት! ከአህጉራችን ምርጥ አምባገነን መሪዎች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሱት የ90 ዓመቱ የዕድሜም የስልጣንም ባለፀጋ፣ የዚምባቡዌው መሪ ሮበርት ሙጋቤ ናቸው።  ፕሬዚዳንቱ አገሪቱ ከቅኝ ግዛት ነፃ ከወጣች ጀምሮ ላለፉት 34 ዓመታት ህዝቡን አንቀጥቅጠው ገዝተዋል። ይሄም ሳያንሳቸው…በቅርቡ ደግሞ የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበርነትን ተረክበዋል፡፡
አንድ ነገር ልንገራችሁ አይደል… በአፍሪካ ህብረት ከምር ተስፋ የቆረጥኩት ሙጋቤን ሊቀመንበር አድርጐ የሾመ ዕለት ነው (ሊቀመንበርነቱን ለሚስቴ አውርሻታለሁ እንዳይሉ ብቻ!) ወዳጆቼ…አያደርጉትም ብላችሁ ጥርጣሬ እንዳይገባችሁ! እንኳን የህብረቱን ሊቀመንበርነት የአገር መሪነቱን እኮ ለውድ ባለቤታቸው ሊያወርሷት ጉድ ጉድ እየተባለ ነው፡፡ (ግን እንዴት አመኗት?!)
በአንድ ወቅት የቢቢሲ ጋዜጠኛ “መቼ ነው ህዝቡን የሚሰናበቱት?” ብሎ ሲጠይቃቸው---- የሰጡትን ምላሽ ሰምታችኋል? (ተጫዋች እኮ ናቸው!) “ህዝቡ ወዴት ሊሄድ ነው?” ነበር ያሉት፡፡ (እሳቸውማ ከዘላለም ሥልጣናቸው ወዴት ይሄዳሉ!?) እንደ እነ ጋዳፊ በህዝብ አመፅ ከስልጣን ከመገርሰስ የተረፉት  ሙጋቤ፤ ከዚህ በኋላ እንኳ ገዳምም ቢገቡ ደንታ የላቸውም፡፡
ለረዥም ዘመን በአምባገነንነት ሥልጣን ላይ በመክረም የሚታወቁት ሙጋቤ ብቻ አይደሉም። በአስሮቹ የአምባገነን ምርጦች (Top 10) ውስጥ ከተካተቱት መካከል የኡጋንዳው መሪ ዩዌሪ ሙሴቪኒ (28 ዓመት!)፣ የሱዳኑ ኦማር ሃሰን አልበሺር (25 ዓመት!)፣ የካሜሩኑ ፖል ቢያ (32 ዓመት!) … ህዝባቸውን ወደ እስከሚጠላ አንቀጥቅጠው ገዝተዋል።
እንዲህ የአህጉሪቱን ታሪክ መበርበር ስትጀምሩ፣ አፍሪካን በእርግጥም የሲኦል እኩያ ያደረጓት የገዛ አምባገነን መሪዎቿ እንጂ የአውሮፓ ቅኝ ገዢዎች እንዳልሆኑ ትረዳላችሁ፡፡ የሴራሊዮን፣ የኮንጐ፣ የደቡብ ሱዳን፣ የሶማሊያ ወዘተ … የእርስ በርስ ግጭትና እልቂት የተከሰተው እኮ በቅኝ አገዛዝ ዘመን አይደለም፡፡ በሰው በላዎቹ የአፍሪካ አምባገነን መሪዎች ጊዜ እንጂ!፡፡
ቀደም ብዬ እንደነገርኳችሁ … የአፍሪካ ህዝብ እርግማን የለበትም፡፡ ለዚህም ነው እንደ ሱዳናዊው የቴሌኮም ቢዝነስ ከበርቴ ሞ ኢብራሂም ያሉ አርቆ አሳቢ አፍሪካውያን የተፈጠሩት፡፡ እኚህ ባለፀጋ የአፍሪካ የመልካም አስተዳደር ሽልማት ፋውንዴሽንን በ2006 እ.ኤ.አ ያቋቋሙት የአፍሪካን ህዝቦች ከሲኦል ኑሮ ለመገላገል ነው፡፡ እናም ህዝቡን ከድህነት አላቆ፣ የኑሮ ደረጃውን አሳድጎ፣ ኮሽታ ሳያሰማ ሥልጣን ለለቀቀ የአፍሪካ መሪ፣ ዳጎስ ያለ ገንዘብ ይሸልማሉ (ዕውቅናው ሳይጨመር!) ዳጎስ ያለ ሲባል … ስንት ትገምታላችሁ? 5 ቢ. ዶላር ነው! (በአበሽኛ 100 ሚ. ብር!) ይሄ ብቻ ግን አይደለም፡፡ ተሸላሚዎቹ በህይወት እስካሉ ድረስ በየዓመቱ 200ሺ ዶላር (2 ሚ. ብር በሉት!) ይሰጣቸዋል፡፡ (ጡረታ በሉት!) በነገራችን ላይ የዘንድሮን የአፍሪካ ስኬታማ አመራር ሽልማት ያሸነፉት የቀድሞው የናምቢያ መሪ ሂፌክ ፑንዬ ፓሃምባ ናቸው፡፡ በ2007 ሽልማቱን የሞዛምቢክ መሪ የነበሩት ጃኪውም አልቤርቶ ቺሳኖ ያሸነፉ ሲሆን በ2008 የቦትስዋናው የቀድሞው ፕሬዚዳንት ፌስቱስ ጎንቴባንዬ ሞጋ ሽልማቱን ወስደዋል፡፡ ማንዴላም በዚያው ዓመት የክብር ሎሬት ተሸላሚ ነበሩ፡፡
በ2011 ደግሞ የኬፕቨርዲ የቀድሞ መሪ ፔድሮ ዲ ቬሮና ሮድሪጉስ ፒሬስ የ5ቢ. ዶላር አሸናፊ ሆነዋል፡፡ የሚገርማችሁ ነገር…ለሶስት ዓመታት (በ2009፣ 2012 እና 2013) ተሸላሚ ባለመገኘቱ ሽልማቱ  ተዘሏል፡፡ (ከስልጣን በሰላም የወረደ ከየት ይምጣ!) ሱዳናዊው ባለፀጋ ይሄን የመሪዎች ሽልማት እንዴት እንዳሰቡት እያሰላሰልኩ ሳለ ሌላ ድንገተኛ ሃሳብ ብልጭ አለልኝ። (ዩሬካ!)
ምን መሰላችሁ? የ2016 የኢብራሂም የአፍሪካ መሪዎች ሽልማትን የአገራችን ጠ/ሚኒስትር የተከበሩ አቶ ኃ/ማርያም ደሳለኝ እንዲያሸንፉ እፈልጋለሁ፡፡ ዓላማዬ ጠ/ሚኒስትሩን በሰበብ ከስልጣን ለማስወረድ አይደለም (ዞሮ ዞሮ እኮ--በመተካካት መውረዳቸው እኮ አይቀርም!) ለማንኛውም የእኔ ሃሳብ … እሳቸውን በማሸለም የአገራችንን መልካም ገፅታ መገንባት ነው። (“Killing two birds with a stone” አለ ፈረንጅ!) አያችሁ…ጠ/ሚኒስትሩ የ5ቢ. ዶላር ሽልማቱን እንዳሸነፉ በየሚዲያው ዜናው ሲናኝ፣ ዓለም ስለ ጦቢያ ያለው አመለካከት ከመቅፅበት ይቀየራል፡፡ (“ካልታዘልኩ አላምንም” አሉ!)
እናም እቺ “ፖለቲከኞችንና ጋዜጠኞችን እንዲሁም የሃይማኖት መብት አቀንቃኞችን ወህኒ ቤት አጉራለች” ተብላ የምትታማ (ሃሜት ልማዳቸው እኮ ነው!) መከረኛ አገራችን፤ ስሟ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የሚታደሰው በእንዲህ ያለው መሬት አንቀጥቅጥ ክስተት ነው---ብዬ አምናለሁ፡፡ ይኼውላችሁ… ጠ/ሚኒስትሩ ድምጽ ሳያሰሙ ከስልጣን ወርደው የሞ ኢብራሂም ፋውንዴሽን ተሸላሚ ሆኑ ማለት በአገሪቱ ላይ መልካም አስተዳደር ለመስፈኑ ጉልህ ማረጋገጫ ነው፡፡ ያኔ የውጭ አገር ኢንቨስተሮች ያለ የሌለ ሃብታቸውን ሰብስበው ጦቢያ እምብርት ላይ ኢንቨስት ለማድረግ እንደጉድ ይሽቀዳደማሉ፡፡ ያኔ ጋዜጠኞችን በማሰርና በማሰደድ እንዲሁም በሰብዓዊ መብት ጥሰት በተደጋጋሚ የምትወነጀለው አገራችን ክሱና ውንጀላው ሁሉ ይሰረዝላታል፡፡ ያኔ የቱሪስቶች ቁጥር ታይቶ በማይታወቅ መጠን ወደ ሰማይ ይመነደጋል። ያኔ የሰብዓዊና የልማት ድጋፎች ከኒዮሊበራል መንግስታት ይጎርፍልናል፡፡ ኢትዮጵያ የ“አፍሪካ ታይገር” መሆኗን እነ Economist, The Guardian, New York Times, Blumberg, Washington Post ወዘተ… በስፋት ይዘግባሉ፡፡ ይተነትናሉ፡፡ (ኢህአዴግም ህልሙ ተሳካለት ማለት እኮ ነው!)
ጠ/ሚኒስትሩ ይሄን ግብ ካሳኩ በኋላ ከፈለጉ በ10 ሚ. ብር ቦንድ (የህዳሴ ግድብ) በመግዛት የግል ባለሃብቱን በአርአያነት ሊያነቃቁ ይችላሉ፡፡ ከዚህ በላይ ህይወት፣ ከዚህ በላይ መስዋዕትነት፣ ከዚህ በላይ ጽናት፣ከዚህ በላይ እርካታ ከየት ይመጣል? ይሄ ሁሉ የሚሳካው ግን ፓርቲያቸው እሺ ካለ ነው። ኢህአዴግ እንደለመደበት ጠ/ሚኒስትሩን አልለቅም ብሎ ክችች እንዳይል ጸሎት ያስፈልጋል (ለቀድሞው ጠ/ሚኒስትርም አልበጃቸውም!)

የተሳሳተና ጎጂ አስተሳሰብ መያዛቸው ነው ችግሩ

   ለግንቦቱ ምርጫ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በተካሄደው ክርክር ላይ የተሳተፉ ሶስት ፓርቲዎች፣ ተመሳሳይ ሃሳቦችን እንዳቀረቡ የሚገልፅ ነበር የዛሬ ሁለት ሳምንት ፅሁፌ። ምን ያህል ተቀራራቢ እንደሆኑ ለማሳየትም፣ ከተከራካሪዎቹ አንደበት በምሳሌነት ጥቂት አባባሎችን ጠቅሻለሁ። ግን ለወቀሳ አልነበረም። እንዲያውም፣ የዋና ዋና ተፎካካሪ ፓርቲዎች  አስተሳሰብ ተቀራራቢ ካልሆነ፣ የምርጫ ፖለቲካ በአጭሩ ከመቀጨት አይድንም።
በእርግጥ፣ ፓርቲዎቹ የተለያየ የአስተሳሰብ አቅጣጫ እንደሚከተሉ ነው የሚናገሩት። ኢህአዴግን በመወከል የተከራከሩት አቶ አባይ ፀሐዬ፣ ፓርቲያቸው ‘አብዮታዊ ዲሞክራሲ’ ወይም ‘ልማታዊ ዲሞክራሲ’ የተሰኘ አስተሳሰብ እንደሚከተል ገልፀዋል - በከፊል የነፃ ገበያ አሰራርን ብንቀበልም መንግስት በኢኮኖሚ ውስጥ በሰፊው ጣልቃ መግባት አለበት በማለት። የመድረክ አመራር አባል ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በበኩላቸው፣ ትክክለኛው አማራጭ የ‘ሶሻል ዲሞክራሲ’ አስተሳሰብ መሆኑን በመጥቀስ፣ ከከፊል የነፃ ገበያ አሰራር ጋር መንግስት በኢኮኖሚ ውስጥ ጉልህ ሚና ሊኖረው ይገባል ብለዋል - መንግስት ከዜጎች ገቢ 50% ያህል ታክስ ሲሰበስብ የሚታይባቸውን አገራት በምሳሌነት በመጥቀስ። ለነፃ ገበያ ስርዓት የተሻለ ትኩረት የሚሰጥ ‘የሊበራል ዲሞክራሲ’ አስተሳሰብን እንከተላለን ያሉት የኢዴፓው ዶ/ር ጫኔ ከበደ በበኩላቸው፣ መንግስት በኢኮኖሚ ውስጥ በተመረጠ አኳሃን ጣልቃ መግባቱ ግን አስፈላጊ እንደሆነ ተናግረዋል።
የፓርቲዎቹን ክርክር የሚከታተል ሰው፣ የፓርቲዎቹን የዝንባሌ ልዩነት መታዘብ እንደሚችል አያጠራጥርም። ነገር ግን፤ ፓርቲዎቹ የካፒታሊዝምና የሶሻሊዝም ሃሳቦችን ያቀላቀለ ተመሳሳሳይ ቅይጥ አስተሳሰብ የያዙ መሆናቸው ሚስጥር አይደለም። በአንድ በኩል ስለ ነፃ ገበያ እየተናገሩ፣ በሌላ በኩል ደግሞ በሰዎች መካከል የሃብት ልዩነትን ለማጥበብ የመንግስት ጣልቃ ገብነት ያስፈልጋል በማለት ፓርቲዎቹ ይስማማሉ። በአንድ በኩል የንብረት ባለቤትነት መብትን እንደሚያከብሩ እየተናገሩ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ሃብት ከሚያፈሩ አምራቾች ላይ ሃብት በመውሰድ ለሌሎች የማከፋፈል አሰራርን እንደሚደግፉ ሲገልፁ፣ “ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል” ወይም “ማህበራዊ ፍትህ” እያሉ ያሞግሱታል። የፓርቲዎቹ የአስተሳሰብ ተመሳሳይነት የዚህን ያህል በግልፅ የሚታይ ነው። ለነገሩ፤ እኔ ሳልሆን ፓርቲዎቹ ራሳቸው በአስተሳሰብ ተቀራራቢ መሆናቸውን በገሃድ ይመሰክራሉ። ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በፋና ሬድዮ በተካሄደ ሌላ ክርክር ላይ እንደገለፁት፣ የሶሻሊዝምና የካፒታሊዝም አስተሳሰቦችን ያዳቀለ ቅይጥ አስተሳሰብ ነው የያዙት። የተወሰነ የነፃ ገበያ አሰራርንና የመንግስት የኢኮኖሚ ገናናነትን ያቀላቀለ ቅይጥ ኢኮኖሚን ነው የሚፈልጉት።
የተዋጣላቸው ተከራካሪ የሆኑት የኢዴፓ መስራች አቶ ልደቱ አያሌው፣ ኢህአዴግ ከጊዜ ወደ ጊዜ አስተሳሰቡን እየቀየረ ወደ ኢዴፓ አስተሳሰብ እየተጠጋ መጥቷል፤ ጥሩ ነው ሲሉ ተናግረዋል - በፋና ሬድዮው ክርክር። የኢህአዴግ ተወካይ አቶ ዛዲቅ አብርሃ በበኩላቸው፣ ተቃዋሚዎች ናቸው አስተሳሰባቸው በመቀየር ወደ ኢህአዴግ አስተሳሰብ እየተቀራረቡ የመጡት ብለዋል። “ማን ተጠጋ?” የሚለውን ጉዳይ አከራካሪ ጥያቄ በማድረግ፣ የፓርቲዎቹን የሃሳብ ልዩነት ለማጉላት እንችል ይሆናል። ግን የዚህችው መከራከሪያ ጥያቄ መነሻ ነጥብ መዘንጋት የለብንም። በአስተሳሰብ ተቀራራቢ መሆናቸውን ፓርቲዎቹ ራሳቸው ያምናሉ። ዋናው ነጥብ ይሄው ነው። አቶ ልደቱ እንዳሉት፣ የፓርቲዎቹ አስተሳሰብ መቀራረቡ ጥሩ ነገር ነው። ለምን?
አንደኛ ነገር፣ ፓርቲዎች የሚፎካከሩበት የምርጫ ፓለቲካ በሰላምና በተረጋጋ ሁኔታ ለረዥም ጊዜ ሊዘልቅ የሚችለው፣ የተፎካካሪ ፓርቲዎች መሰረታዊ አስተሳሰብ ተቀራራቢ ከሆነ ብቻ ነው። አለበለዚያ፣ አስተሳሰባቸው በእጅጉ የተራራቀ ከሆነ፣ አንዱ በምርጫ ተሸንፎ ሌላው ስልጣን ላይ በወጣ ቁጥር በ“ስር ነቀል ለውጥ” አገር ይታመሳላ። ስልጣን ላይ በተፈራረቁ ቁጥር አገሪቱ በ‘አብዮት’ አዙሪት የምትመሳቀል ከሆነች፣ የምርጫ ፓለቲካ ከጊዜያዊ ፋሽንነት ያለፈ እድሜ አይኖረውም። በሌላ ምሳሌ ለማስረዳት ያህል፣ የምግብ አሰራር ውድድር፣ በተለያዩ የምግብ ጣዕሞችና አይነቶች መካከል መሆን አለበት እንጂ፣ ውድድሩ በምግብ እና በአይነ ምድር መካከል ከሆነ ከአንድ ሙከራ በላይ አይዘልቅም። በሌላ አነጋገር፣ ውድድሩ የኮካና የፔፕሲ መካከል ሳይሆን፤ በለስላሳ መጠጥና በመርዝ መካከል እንዲሆን የምንጠብቅ ከሆነ፣ የምንፈልገው ወይም የሚበጀን ነገር ያልገባን አላዋቂዎች ሆነናል ማለት ነው። ከዚሁ ነጥብ ሳንወጣ ሁለተኛውን ቁምነገር ማስተዋል እንችላለን።
የተረጋጋ ስልጡን የምርጫ ፓለቲካ ለዘለቄታው እውን እንዲሆን፣ ሰፊ ድጋፍ ያላቸው ተፎካካሪ ፓርቲዎች በመሰረታዊ አስተሳሰብ ተቀራራቢ ሊሆኑ ይገባል። ይሄ የመጀመሪያው ቁምነገር ነው። ግን፣ ተቀራራቢ መሆናቸው ብቻ በቂ አይደለም። ለምሳሌ፣ ከአርባ አመት በፊት በአገራችን የነበሩ ዋና ዋና ፓርቲዎች፣ ተመሳሳይ የአስተሳሰብ ቅኝትን የተከተሉ እንደነበር ይታወቃል - ኢህአፓ፣ መኢሶን ወዘተ..። እጅጉን ተቀራራቢ ከመሆናቸው የተነሳ፣ አንዱን ከሌላው ለመለየት ያስቸግራል - የለየላቸው ሶሻሊስቶች (ኮሙኒስቶች) በመሆናቸው። ግን፣ ስልጡን የፖለቲካ ምርጫ አልተፈጠረም። ለምን? አስቡታ! የአንድ ፓርቲ አምባገነንነት መስፈን አለበት የሚል ተመሳሳይ አስተሳሰብ የያዙ ፓርቲዎች፣ በጭራሽ በጭራሽ ብዙ ፓርቲዎች የሚፎካከሩበት የምርጫ ፓለቲካ ሊፈጥሩ አይችሉም። የሁሉንም ሰው እውቀትና ንግግር እየተቆጣጠረ የሚያፍን፣ የሁሉም ሰው ኑሮና ንብረት ላይ እያዘዘ የሚወርስ፣ የሁሉም ሰው ማንነትና ሰብእና ላይ አድራጊ ፈጣሪ ሆኖ የሚገዛ አምባገነን መፈጠር እንዳለበት ተስማምተው የለ! ‘እኔ አምባገነን ልሁን’፣ ‘እኔ ልሁን’ እያሉ ይጨፋጨፋሉ፣ ይጨፈጭፋሉ እንጂ፣ እንዴት ብለው የተረጋጋ ስልጡን የምርጫ ፖለቲካ ይፈጥራሉ? ሁለተኛው ቁምነገር ይሄው ነው። ፓርቲዎቹ በአስተሳሰብ መቀራረባቸው ብቻ ሳይሆን፣ ቅርርባቸው በስልጡን የነፃነት አስተሳሰብ ዙሪያ መሆን አለበት።
አሳዛኙ ነገር፤ የአገራችን ፓርቲዎች በስልጡን የነፃነት አስተሳሰብ ዙሪያ ሳይሆን በቅይጥ አስተሳሰብ ዙሪያ ነው የተቀራረቡት። ይበልጥ አሳዛኝና አሳሳቢ የሚሆነው፤ በአለም ዙሪያ የሚታየው አዝማሚያም ተመሳሳይ ነው - ደረጃው ቢለያይም ከሞላ ጎደል ሁሉም አገራት በ“ቅይጥ አስተሳሰብ” ውስጥ የሚተራመሱ ሆነዋል። ከኮሙኒስት ኩባ እና ከቻይና ጀምሮ፣ እስከ ደቡብ አፍሪካና ቬኒዝዌላ... ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከኢትዮጵያ እስከ ራሺያና ህንድ፣ ከናይጄሪያ እስከ ፈረንሳይና ጃፓን፣ ከብራዚል እስከ ግሪክና ስፔን፣ ከግብፅ እስከ እንግሊዝና አሜሪካ... የቀረ አገር የለም ማለት ይቻላል። የኢኮኖሚ መስክን ብቻ ብንመለከት፣ በአንድ በኩል በነፃ ገበያ ስርዓት፣ አስገራሚ የቴክኖሎጂ ፈጠራዎችንና የምርታማነት እመርታዎችን፣ የየብልፅግና ለውጦችንና የኑሮ እድገትን እናያለን። በሌላ በኩል ደግሞ የነፃ ገበያ ስርዓትን በሚሸረሽር የመንግስት ጣልቃ ገብነት ሳቢያ፣ ቅጥያጣ ድጎማንና የታክስ ጫናን፣ የመንግስታት የእዳ ክምርንና የፋይናንስ ቀውስን፣ የሃብት ብክነትንና ሙስናን፣ ስራ አጥነትንና አመፅን እናመለከታለን። በአጭሩ፣ ከብልፅግና እድል ጋር፣ የጥፋት አፋፍ ላይ የደረሰ የኢኮኖሚ ቀውስ የእለት ተእለት ትዕይንት ሆኗል። የሁለት አገራትን ሙከራ ብቻ በጨረፍታ እንመልከት። በቅድሚያ ኩባን።
አብዛኛው የኩባ ሰራተኛ ወደ ሃያ ዶላር ገደማ የወር ደሞዝ እንደሚያገኝ የገለፀው የኒውስዊክ የትናንት እትም፣ የአንጋፋ ሃኪሞች ደሞዝ በቅርቡ ተሻሽሎ ወደ 70 ዶላር (ወደ 1500 ብር) ግድም የደረሰላቸው ቢሆንም የአብዛኞቹ ዶክተሮች ደሞዝ ግን 26 ዶላር (ወደ 600 ብር የሚጠጋ) እንደሆነ ዘግቧል።
የሃኪሞቹ ደሞዝ ከአብዛኛው ሰራተኛ ደሞዝ ያን ያህልም አይለያይም። ለምን? በፅዳት ሰራተኞችና በህክምና ዶክተሮች መካከል የገቢ ልዩነት እንዳይኖር ለማድረግ ነው - “ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል”፣ “ማህበራዊ ፍትህ” ይሉታል ሶሻሊስቶቹ። በአገራችን ፖለቲከኞች ዘንድ የሚዘወተሩ አባባሎች እንደሆኑም ታዝባችሁ ይሆናል። ያው፣ በሰዎች መካከል የቁመት ወይም የብልህነት ልዩነት እንዳይኖር፣ ረዣዥሞቹን መከርከም ወይም ብሩህ አእምሮዎችን ማደብዘዝ እንደማለት ነው። ይህንን ነው ፍትህ የሚሉት። የ50 ዓመቱ ኩባዊ ራፋኤል ግን፣ ለ“ማህበራዊ ፍትህ” የመስዋዕት በግ መሆን አንገሽግሿቸዋል። በወጣትነት እድሜያቸው በህክምና ተመርቀው መስራት የጀመሩ ጊዜ ምንኛ እንደተደሰቱ ባይረሱትም፣ ዛሬ ግን እንደ ሩቅ ዘመን ትዝታ ነው የያኔ ሙያቸውን የሚያስታውሱት። ስራቸውን ለቅቀው ከወጡ አምስት ስድስት አመታት ተቆጥረዋል። በእርግጥ አንዳንዴ፣ የህክምና ሙያቸውን ሲያስታውሱት፣ ከትዝታነትም አልፎ ያንገበግባቸዋል - ከሚወዱት ሙያ በመለየታቸው። ግን ሌላ አማራጭ አልነበራቸውም። በ12 ዶላር (250 ብር ገደማ) ደሞዝ የህክምና ሙያቸውን እንደጀመሩ የሚናገሩት ራፋኤል፣ ከበርካታ አመታት በኋላ ደሞዛቸው ወደ 15 ዶላር “እንዳደገ” ይገልፃሉ።
በእርግጥ ለአርባ አመታት ኩባን አንቀጥቅጠው የገዟት ፊደል ካስትሮ በእርጅናና በህመም ምክንያት ከስልጣናቸው ከተነሱ ወዲህ፤ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ አንዳንድ የለውጥ ጭላንጭሎች መታየት ጀምረዋል። የጀማሪ ዶክተሮች ደሞዝ እንኳ ወደ 600 ብር የሚጠጋ ሆኖላቸው የለ! ይሄ፣ በምድረ ኩባ “አጀብ” የሚያሰኝ ለውጥ ነው። ራፋኤል ግን፣ አሁንም ፈፅሞ አልተዋጠላቸውም። የለውጥ ጭላንጭል እየተፈጠረ መሆኑን አይክዱም። እንደ ድሮ ቢሆን ኖሮ፣ መንግስት ከመደበላቸው የስራ ቦታ መልቀቅ ባልቻሉ ነበር። ዛሬ ግን ይቻላል። ሁሉም ነገር በመንግስት ተይዞ በቆየበት አገር፣ ትንንሽ ሱቆችን መክፈት ተፈቅዷል። አንዳንድ ሃኪሞች፣ በሱቅ ንግድ መተዳደርን ቢመርጡ ምን ይገርማል?
ራፋኤል ግን፣ የታክሲ ሾፍርናን ነው የመረጡት። የግል ታክሲ ተፈቅዷላ። ቱሪስቶች በብዛት እንዲገቡ መፈቀዱ ደግሞ ጠቀማቸው። ዛሬ አቶ ራፋኤል በታክሲ ሹፍርና በወር ከ200 ዶላር በላይ ገቢ ያገኛሉ። ልጄ በህክምና ተመርቆ ሥራ ጀምሯል የሚሉት ራፋኤል፣ ነገር ግን ልጃቸው በህክምና ሙያው ከሚያገኘው ደሞዝ ይልቅ እሳቸው በታክሲ ሹፍርና የሚያገኙት ገቢ በአስር እጥፍ ገደማ እንደሚበልጥ ጠቁመዋል። ግን እሱም ሞኝ አይደለም። በእረፍት ቀናት አባቱን በመተካት የታክሲ ሹፍርና እንዲሰራ ሲጠይቁት አላቅማማም - ለሁለት ቀን ሰርቷል። “30 ዶላር ከፍየዋለሁ፤ በወር ከሚያገኘው ደሞዝ ይበልጣል” ብለዋል ራፋኤል። የቅይጥ ኢኮኖሚ ነገር እንዲህ ነው።
ያለ ጥርጥር የዛሬው ቅይጥ ኢኮኖሚ፣ ከትናንቱ “ያልተበረዘ የሶሻሊዝም ኢኮኖሚ” ይበልጣል። ግን አስቡት። የህክምና ዶክተር ከመሆን ይልቅ፤ የታክሲ ሾፌር መሆን ይሻላል - ገቢያቸው የትና የት! ነገር ግን የሃኪምና የሾፌር ገቢ መለያየቱና መራራቁ ወይም የታክሲ ሾፌር በወር 200 ዶላር ገቢ ማግኘቱ አይደለም ችግሩ። ከሃኪሞች ተቀንሶ አይደለም የሾፌሮች ገቢ የጨመረው። እንዲያውም፤ የታክሲ ስራን ጨምሮ በጥቂት መስኮች የግል ቢዝነስ በመፈቀዱ ምክንያት የተፈጠረው ለውጥ፣ እንደ ራፋኤል ለመሳሰሉ የታክሲ ሾፌሮች ብቻ ሳይሆን ለሃኪሞችም በተወሰነ ደረጃ ጠቅሟል። እናም፣ ብዙ ነው ባይባልም፣ የሃኪሞች ደሞዝ ትንሽ እንዲሻሻል ግፊት በማሳደር አስተዋፅኦ አበርክቷል። ምናልባት ወደፊት ደግሞ የግል ክሊኒክና ሆስፒታል ሲፈቀድ፣ የሃኪሞች ገቢ ሙያቸውንና ስራቸውን የሚመጥን የሚሆንበት እድል ይፈጠራል። በኩባ አሁን የታየችው የነፃ ገበያ ጠባብና ቁንፅል ጭላንጭል፣ የዚያችኑ ያህል ትንሽዬ የኑሮ ለውጥ እንደፈጠረችው ሁሉ፤ በጭላንጭሏ የገባው ብርሃን እየደመቀ የነፃ ገበያ ስርዓት እየሰፋና እየጨመረ ቢመጣ፤ የዚያኑን ያህል ከሶሻሊዝም የድንዛዜና የድህነት የሚላቀቁበት ሰፊ የእድገትና የብልፅግና እድል ይፈጠራል። አለበለዚያ ግን፤ “መማር ከንቱ” የሚያስብል፣ በጅምር የቅይጥ ኢኮኖሚ ሳቢያ የሚፈጠር ቀውስ ውስጥ ተዘፍቃ፣ የብልፅግና ጭላንጭሏ በአጭሩ ተቀጭቶ የኋሊት ትንሸራተታለች።
በሌላ አነጋገር፣ ቅይጥ ኢኮኖሚ፣ ወደ በለጠ የነፃ ገበያ ስርዓት የሚያመራ ጊዜያዊ የመሸጋገሪያ ክስተት ከመሆን አልፎ፤ ቋሚ ስርዓት እንዲሆን መመኘት ውሎ አድሮ የኢኮኖሚ ቀውስን ከመጋበዝ የተለየ ትርጉም አይኖረውም። በአሜሪካና በምዕራብ አውሮፓ፣ ከዚያም በእነ ታይዋንና ደቡብ ኮሪያ፣ ባለፉት 20 ዓመታት ደግሞ ፖላንድና ቼክ በመሳሰሉ የምስራቅ አውሮፓ አገራት እንደታየው፤ የነፃ ገበያ ስርዓትን ተግባራዊ ባደረጉት መጠን ነው ብልፅግና እውን የሚሆነው።
ቻይናም ከረሃብ ለመላቀቅና ወደ ብልፅግና ጎዳና የመግባት እድል ያገኘችው፤ በሌላ ምክንያት አይደለም። ከጊዜ ወደ ጊዜ የመንግስት ቁጥጥርን እየቀነሰች፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ የነፃ ገበያ አሰራርን ስታስፋፋ ስለቆየች ነው፤ ለ30 አመታት ያለማቋረጥ ከአስር በመቶ በላይ የኢኮኖሚ እድገት ስታስመዘግብ የቆየችው። በእርግጥ ባለፉት አራት አመታት የኢኮኖሚ እድገቱ ረገብ ብሏል፤ ወደ 7.5% ገደማ። ዘንድሮና በሚቀጥለው አመት የኢኮኖሚ እድገቱ ወደ 7 በመቶ እንደሚወርድ የገለፀው የቻይና መንግስት፤ የመቀዛቀዝ አዝማሚያው እንዳይባባስ ስጋት ቢያድርበት አይገርምም። የኢኮኖሚ እድገት ካላስመዘገበ፣ ስልጣን ላይ የመቆየት አቅሙ እንደሚሸረሸር አልጠፋውም። እና ምን ተሻለ?
የቻይና መንግስት ለበርካታ አመታት የነፃ ገበያ አሰራርን እያስፋፋ ቢመጣም፤ አሁንም ኢኮኖሚው ውስጥ የመንግስት ቁጥጥርና ድርሻ ግዙፍ ነው። ማለትም፤ ቅይጥ ኢኮኖሚ። ይህንኑ በቋሚነት ለመያዝ፤ “እስከ ዛሬ ድረስ በተወሰነ ደረጃ ተግባራዊ ያደረግሁት የነፃ ገበያ አሰራር በቂ ነው” ብሎ አሁን ባለው የቅይጥ ኢኮኖሚ ስርዓት መቀጠል እንደማይችል የአገሪቱ ባለስልጣናት ገብቷቸዋል። ለዚህም ይመስላል፣ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ባለፈው ሳምንት በሰጡት ረዥም ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ፣ እስካሁን እንዳደረግነው የነፃ ገበያ አሰራርን በማስፋፋት እንቀጥላለን ያሉት። ለቢዝነስ ድርጅቶች የታክስ ቅነሳ እንደሚደረግ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቅሰው፤ የቢዝነስ ድርጅት የሚያቋቁሙ ሰዎች ላይ የተንዛዛ የቁጥጥርና የምዝገባ ቢሮክራሲ በግማሽ ቀንሰነዋል፤ አሁንም እንደገና በግማሽ እንቀንሰዋለን ብለዋል። ይበጃቸዋል! በቅይጥ አስተሳሰብ ተተብትቦ፣ ቅይጥ ኢኮኖሚን እንደ ቋሚ ስርዓት ይዞ ለመቀጠል መሞከር፣ መጨረሻው አያምርማ። የአገራችን ፓርቲዎችም፣ በጊዜ ይህንን እውነታ ቢገነዘቡ ይሻላቸዋል፤ ለሌሎቻችንም ይሻለናል።

Saturday, 28 March 2015 09:02

የፀሐፍት ጥግ

ሳንሱር፤ ህፃን ልጅ ስቴክ (የተጠበሰ ስጋ) ማኘክ አይችልም በሚል አዋቂን ሥጋ እንዳይበላ መከልከል ነው፡፡
ማርክ ትዌይን
ይህች ዓለም የሌላ ፕላኔት ሲኦል ሳትሆን አትቀርም፡፡
አልዶስ ሁክስሌይ
ከመርህዎች በላይ ለጥቅሞቹ ዋጋ የሚሰጥ ህዝብ ሁለቱንም ያጣቸዋል፡፡
ዲዋይት ዲ. አይዘአንአወር
ህይወት አስደሳች ነው፡፡ ሞት ሰላማዊ ነው፡፡ አስቸጋሪው ሽግግሩ ነው፡፡
አይሳክ አሲሞቭ
እንቅልፍ ኦፔራን የማዳመጫ ግሩም መንገድ ነው፡፡
ጄምስ ስቲፈንስ
ሁሉም ነገር በቁጥጥር ሥር የዋለ ከመሰለ በፍጥነት እየተጓዝክ አይደለም፡፡
ማርዮ አንድሬቲ
ኮስታራ መስለህ ለመታየት ትችላለህ፤ ተጫዋች መስለህ መታየት ግን አትችልም፡፡
ሳቻ ጉይትሪ
የተሳሳተ ጥያቄ ስትጠይቅ ካገኙህ፣ ለመልሱ መጨነቅ አይኖርባቸውም፡፡
ቶማስ ፒንቾን
ፈር ቀዳጅን ጀርባው ላይ ባሉት ኢላማ መምቻ ቀስቶቹ ትለየዋለህ፡፡
ቢቨርሊ ሩቢክ
መደምደሚያ፤ ማሰብ የሚደክምህ ቦታ ነው።
ያልታወቀ ሰው
መፃህፍት በሚቃጠሉበት ቦታ፣ የሰው ልጆችም እጣፈንታ መቃጠል ይሆናል፡፡
ሄይንሪክ ኼይን
አደገኛ መሳሪያዎችን ከጅሎች እጅ በማራቅ እስማማለሁ፡፡ ለምን በመተየቢያ ማሽኖች አንጀምረውም፡፡
ፍራንክ ሊሎይድ ራይት

Published in የግጥም ጥግ

ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ቆቅ ሰባት ልጆቿን ይዛ ከቤት ወጥታ መንገድ ትጀምራለች፡፡
1ኛዋ ጫጩት - እማዬ ወዴት ነው የምንሄደው?
እናት - ቆቅ - ወደሩቅ አገር
2ኛዋ ጫጩት - እዚያ አገር ምን አለ?
እናት ቆቅ - የተሻለ ኑሮ
3ኛዋ ጫጩት - የተሻለ ኑሮ ምንድን ነው?
እናት ቆቅ - የተሻለ ምግብ፣ የተሻለ መጠለያ፣ የተሻለ ወጥቶ - መግባት
4ኛዋ ጫጩት - በመሬትም በአየርም እንደልባችን የመብረር መብት አለን?
እናት ቆቅ - አዎ፡፡ እንደልብ መሮጥ፣ እንደ ልብ መናገር፣ እንደልብ ሀሳባችሁን የመግለጥ፣ የምትወዱን መውደድ፣ የምትጠሉትን መጥላት ትችላላችሁ፡፡
5ኛዋ ጫጩት - የፈለግነው ከተማ ሄደን መኖርስ እንችላለን?
እናት ቆቅ - በደንብ ትችላላችሁ፡፡
6ኛዋ ጫጩት - ትንሽ ትልቅ፣ ቆንጆ አስቀያሚ፣ የተማረ፣ ያልተማረ፣ የዚህ ወፍ ዝርያ የዚያ ወፍ ዝርያ ብለው፤ አንዱን ጠቅመው ሌላውን ጎድተው አያዳሉብንም?
እናት ቆቅ - እንደሱ ቀርቷል፡፡ ጅግራም ሆናችሁ ቆቅ፣ ቁራም ሆናችሁ አሞራ፣ ወፍም ሆናችሁ ወማይ፣ ሣቢሳም ሆናችሁ ጥምብ አንሳ እንደየ ዝርያችሁ የመኖር መብት አላችሁ፡፡ በዝርያችሁ የሚነካችሁ ምንም የለም፡፡
7ኛዋ ጫጩት - እነዚህ የዘረዘርሺልን እርስ በርስ ቢጣሉስ ማን ያስታርቃቸዋል?
እናት ቆቅ - የሁሉም የበላይ የሆነ የአዕዋፍ ንጉሥማ ይኖራል፡፡ ያለንጉሥ መኖርማ አይቻልም፡፡
ይህን እየተጨዋወቱ መንገድ እያቆራረጡ ሄደው ዋናው አውራ ጎዳና ጋ ደረሱ፡፡ አውራ ጎዳናውን ከጠርዝ ጠርዝ በወርዱ አንድ ዘንዶ ተጋድሞበታል፡፡ እናት ቆቅ ዘላ ለመሄድ አልደፈረችም፡፡ ስለዚህ የተኛውን ዘንዶ ቀስቅሳ “ለምን ተኛህ?” ልትለው ፈለገች፡፡ አንገቱን በኩምቢዋ ነካ ነካ አደረገችና፤
“አያ ዘንዶ ምነው በደህና ነው የተኛኸው?” አለችው፡፡ ዘንዶው ለምን እንደተኛ አስቦ አስቦ፤
“ርቦኝ ነው የተኛሁት” አላት፡፡
“እንግዲያው ልጆቼን ልስጥህና ጥገብ፡፡ እኔን ተወኝ” አለችው፡፡
ልጆቿን ዋጠ፡፡ እሷ ተሻግራው ሄደች፡፡
ዘንዶው ጫጩቶቿን በልቶ አላበቃም፡፡ ሀሳብ ያዘው፡፡ “ይቺ ቆቅ እንዴት አምና ልጆቿን ብላ አለችኝ፡፡ ነገር ቢኖራት ነው” አለ፡፡ ቢያስበው ቢያስበው ለተንኮል ነው ብሎ ያሰበው ነገር አልመጣ አለው፡፡ በመጨረሻ፤
“እኔ ምን አሳሰበኝ? እራሷን ብበላት እገላገል የለም እንዴ?” አለና ሲምዘገዘግ ወደ ቆቋ ሄደ፡ ያዛትና “ዓላማሽ ምን እንደሆነ ስላልገባኝ መፍትሔው ራስሽን መዋጥ ነው” ብሎ፤ በልቷት ተገላገለ!
*       *      *
ከማይጠግብ ዘንዶ ይሰውረን፡፡ ልጅም ሰውቶ ራስን ከማጣት ያድነን፡፡ በተጓዝን ቁጥር የተኛ ዘንዶ ከማግኘት፣ እሱን ሳይቸግረን ቀስቅሰን ከመዋጥ የሚጠብቀንን ይዘዝልን፡፡ የማይፈራውን ፈርተን፣ የተኛውን ቀስቅሰን፣ ትውልዳችንን ገብረን፣ የተደሰትን መስሎን ዘራፍ ከማለት ግብዝነት ይሰውረን፡፡
ወደድንም ጠላንም ዘንዶው ዘንዶ ነው! መንገዱን የዘጋው በራሱ ተማምኖ ነው፡፡ ዓመታት መቁጠርና ዘንዶውን “ምስህ ምንድን ነው?” ብለን እንደ ቅድመ ታሪክ ዘንዶ መገበር ሳይሆን መብሰል፣ ራስን ማወቅ፣ ራስን መቻል፣ በራሴ መተዳደር እችላለሁ ማለት ያሻል፡፡
የሀገር ጉዳይ፤ “ያለቀበት” የሚባል የጉልበት ገበያና “ሁሉንም በአምሥት …” የሚባል ዓይነት ንግድ መሆን የለበትም፡፡ ትግልም፣ ልማትም፣ ዲሞክራሲም የሂደት ጉዳይ ነው፡፡ ቁርጥም ነገር፣ ቆረጣም ነገር የለበትም፡፡ እየተወራረደ፣ እየተሞራረደ የሚጠራ፣ የሚሻሻል፣ የሚለወጥ ሂደት ነው!! ዘመን መቁጠር “አዲስ ፍሬ ምን ያህል አፈራሁ?” የማለት የጠራ ዕድገት ከሌለበት እንደው “ዕድሜዬ ይሄን ያህል ነው ከማለት አያልፍም!”
የየራሳችንን የውስጥ ችግር ሳንፈታ ዕድሜዬ ይሄን ያህል ነው ብለን መፎከር የባሰ ምስቅልቅል ችግር ውስጥ መዘፈቅ ነው፡፡ ለአቅመ አዳም ከደረሰ በኋላ ቤተሰቦቹ ጋ የሚኖር ልጅ ከተጧሪ አንድ ነው!
“ፍሬ በስሎ የሚበላው
ወይ በራሱ ጊዜ ሲወድቅ፣ ወይ እኛ ስንለቅመው ነው”
እንደሚባል የገባው ዕውነተኛ ብስለት ያለው ነው፡፡ የውስጥ ደም መፍሰስ (Internal Bleeding) ከአዲስ ደም መቀበል (New Blood Injection) ጋር አይገናኝምና መጀመሪያ የአንጎል ውስጥ ደም ፍሰቱን መገላገል ዋና ነገር መሆኑን ማስተዋል ነው!
“እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው!” ዓይነት አስተሳሰብ የትም አያደርሰንም፡፡ ጊዜን ባግባቡ መለካት ነው የፖለቲካ ቁም ነገር!
ቅዱስ አውግስቶስ ኑዛዜ (Confession) በተባለ ግጥሙ፤
ምንም ነገ ባያልፍ፤ ትላንትና የለም
ምንም ድርጊት ባይኖር፣ ነገ አይፈጠርም
ዛሬም ነገር ባይኖር፣ መኖርን አናቅም
ያለፈው፣ የመጪው፣ የአሁን ውዝዋዜ
ጊዜ ማለት ያ ነው፣ ያ ነው ለእኔ ጊዜ!
በዓላትን ስናከብር የሠራነውን ፍሬ - ነገር እናስተውል፡፡ ፈንጠዝያን ከብስለት እንለይ! አለበለዚያ፤ “ሞኝ ሁለቴ ይነደፋል፡፡ አንዴ እባብ ሲነድፈው፣ አንዴ እባቡን ሲያሳይ” የሚባለው ተረት ሰለባ እንሆናለን! የኋሊት ወደ ታሪክ ሳይሆን ወደፊት፣ ታሪክ ወደ መስራት እንጓዝ!!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

      በኤርትራ የወርቅ ማምረቻና ወታደራዊ ካምፕ ላይ የኢትዮጵያ አየር ሃይል ጥቃት መፈፀሙን የተለያዩ ድረገፆችና ሚዲያዎች ቢዘግቡም የኤርትራው ፕሬዚዳንት ቃል አቀባይ ጥቃቱ አልተፈፀመም ሲሉ ማስተባበላቸውን “ጊስካ አፍሪካ ኦንላይን” ጠቁሟል፡፡
“ቢሻ የወርቅ ማዕድን ማምረቻም ሆነ ወታደራዊ ካምፑ በኢትዮጵያ አየር ሃይል አልተደበደበም” ብለዋል ቃል አቀባዩ ለድረ ገፁ በሰጡት መረጃ፡፡
የሱዳኑ ጋዜጣ “ሳሀፋ” ሰሞኑን ባሰራጨው ዘገባ፤ የኢትዮጵያ አየር ሃይል ከአስመራ በ150 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘውንና የካናዳ ኩባንያ የሆነውን ቢሻ የወርቅ ማእድን ማምረቻ መደብደቡን ሲገልፅ፣ “አሰና” የተሰኘ ድረ ገፅ በበኩሉ፤ ቢሻ የወርቅ ማእድን ማምረቻና ማይ እዳጋ በተባለ ቦታ የሚገኝ ወታደራዊ ካምፕ በኢትዮጵያ አየር ሃይል ወታደራዊ ጥቃት እንደተፈፀመባቸው ዘግቧል፡፡
ኢትዮጵያ በኤርትራ ላይ  ወታደራዊ ጥቃት ፈፅማለች ወይ በሚል ከአዲስ አድማስ የተጠየቁት የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅህፈት ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል በሰጡት ምላሽ፤ “ተጎዳን የሚል ይፋ አቤቱታ ሳይቀርብ እንዳልጎዳችኋቸው ማረጋገጫ ስጡ ማለት አግባብነት የለውም” ብለዋል፡፡”  
የቢሻ ወርቅ ማምረቻ አብላጫ ድርሻውን የያዘው “ኔቭሱን” የተባለው የካናዳ ኩባንያ ሰሞኑን በድረገፁ ባሰፈረው መረጃ፤ የወርቅ ማዕድን ማምረቻው በተፈፀመበት ዝርፊያና በዕድሳት ምክንያት  ለተወሰነ ጊዜ ሥራ አቁሞ እንደነበር ጠቁሞ በቅርቡ ወደ ስራው እንደሚመለስና ዝርፊያውን በተመለከተ የኤርትራ የፀጥታ ሃይሎች ምርመራ እያካሄዱ እንደሆነ አስታውቋል፡፡

Published in ዜና

የአሜሪካ መንግስት ኢትዮጵያ፣ ግብጽና ሱዳን በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ ያለባቸውን አለመግባባት ለመፍታትና ፍትሃዊ የውሃ ክፍፍል እንዲረጋገጥ ለማድረግ ባለፈው ሰኞ የፈረሙትን የትብብር ስምምነት እንደሚያደንቅ ማስታወቁን ኢጂብት ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
የአሜሪካ መንግስት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጄን ፓስኪ ባለፈው ረቡዕ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፣ አሜሪካ ሶስቱ አገራት በአባይ ወንዝ የውሃ ድርሻ ላይ የሚያነሱትን ጥያቄ በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ያስችላል የተባለውን ስምምነት፣ አገራቱ በጉዳዩ ዙሪያ አንድ እርምጃ መራመዳቸውን የሚያሳይ ጠቃሚ ሁነት በመሆኑ ታደንቀዋለች ብለዋል፡፡
መንግስታቸው በአገራቱ መካከል የትብብር መንፈስ እንዲፈጠር ለማድረግና የሁሉንም አገራት ጥቅም ባስጠበቀ መልኩ አባይን በዘላቂነት ለማልማት ከኢትዮጵያ፣ ከግብጽና ከሱዳን ጋር በትብብር እንደሚሰራም አስታውቀዋል፡፡
ሶስቱ አገራት የአባይን ውሃ በፍትሃዊነት መጠቀም የመቻላቸው ጉዳይ፣ በአገራቱ መካከል ዋነኛ የውጥረት መንስኤ ሆኖ መቆየቱን የጠቆመው ዘገባው፣ የተፈረመው ስምምነት በሁሉም አገራት የውሃ ደህንነት ላይ ጉዳት እንዳይከሰት የሚያደርግ መሆኑንና ግብጽና ሱዳን ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ይፋዊ እውቅና መስጠታቸው የታየበት ነው መባሉን አመልክቷል፡፡
በሌላ በኩል በአዲስ አባባ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስ መምህር የሆኑት አቶ ዳር እስከዳር ታዬም፤ የግብጹ ፕሬዚዳንት ወደ ድርድር መምጣታቸውና የግድቡን መገንባት አለመቃወማቸው ከዚህ በፊት አገራቸው ስታራምደው ከነበረው አቋም የተለየና አንድ እርምጃ ወደፊት የተራመደ ነው ብለዋል፡፡ የትብብር መንፈሱ ጠቃሚነት እንዳለው የጠቆሙት ምሁሩ፣ የትብብሩ መንፈስ እውነት መሆንና አለመሆን ግን በስምምነቱ አፈጻጸም ላይ የሚታይ ይሆናል ብለዋል፡፡
የቀድሞው የኢዴፓ ሊቀመንበር አቶ ልደቱ አያሌው በበኩላቸው፤የግብጹ ፕሬዚዳንት የአባይን ውሃ ከፈጣሪ እንደተበረከተ የግል ስጦታ ከማየት አስተሳሰብ ተላቀው፣ ውሃው የሌሎች አገራትም ሃብት እንደሆነ እውቅና መስጠታቸውን አድንቀው፣ስምምነቱን መፈረማቸው ብስለታቸውን ያሳያል ብለዋል፡፡ “ትብብሩ የሁለቱንም አገራት ህዝቦች በሚጠቅም መልኩ እንዲቀጥል ማድረግ ይገባል፤ የአልሲሲ ጅምር መልካም ቢሆንም ውጤቱ በሂደት የሚታይ ይሆናል” ሲሉ አቶ ልደቱ አስተያየታቸውን ገልጸዋል፡፡

Published in ዜና
Page 3 of 21