የግል ጋዜጦች፤ ብርሃንና ሰላም  ለኪሳራ እየዳረገን ነው ብለዋል     
ጋዜጣውን “እንዝጋው አንዝጋው” በሚለው ላይ እየተነጋገርን ነው - ኢትዮ ቻናል
ጋዜጣችን ሁለትና ሦስት ቀን ዘግይቶ ስለሚወጣ ዜና መስራት ትተናል - ካፒታል
  ብርሃንና ሰላም የደንበኞች ቅሬታ ለመፍታት እየሰራሁ ነው ብሏል
ብርሃንና ሰላም ከደንበኞች ጋር “ተጠያቂ የሚያደርገኝን” ውል እፈራረማለሁ አለ
የጋዜጦች ሕትመት መዘግየት  እስከ ነሐሴ ድረስ  ሊዘልቅ ይችላል ተባለ

      ከሀረማያ ዩኒቨርስቲ በግብርና ትምህርት ተመርቀው የግብርና ባለሙያ የሆኑት አቶ ፍቃዱ ታመነ፤ ከ1995 ዓ.ም ጀምሮ የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ቋሚ ደንበኛ እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ቅዳሜ ጠዋት ጋዜጣውን  ለመግዛት ወደ ፒያሳ በተደጋጋሚ ቢመላለሱም “አርፍዷል፤ አልወጣም” የሚል ምላሽ እያገኙ ባዶ እጃቸውን ወደ ቤታቸው ይመለሳሉ፡፡ እሁድ እሁድ ደግሞ ከቤታቸው መውጣት አይወዱም፡፡  በዚህ ምክንያት ጋዜጣውን ካነበብኩ ሰነባበትኩ ይላሉ፡፡ “አዟሪዎችን ስጠይቅ እሁድ ይወጣል ቢሉኝም እኔ ግን ቅዳሜ በትኩሱ ማግኘት ያለብኝን አዲስ አድማስ እሁድ ለመግዛት ሞራል የለኝም፤ ምክንያቱም ያደረ ምግብ ይመስለኛል” በማለት ጋዜጣው ለምን ቀኑን ጠብቆ እንደማይወጣ ይጠይቃሉ፡፡
በአንድ የመንግስት መስሪያ ቤት ውስጥ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ የሆነውና ስሙ እንዲገለፅ ያልፈለገው  ወጣት፤ አዲስ አድማስ፣ ሪፖርተር፣ ፎርቹን፣ ካፒታል፣ ሰንደቅ… ጋዜጦችንና ሌሎች መፅሔቶችን በደንበኝነት ወደ ቢሮው እንደሚያስመጣ ጠቁሞ፣ ከጥቂት ወራት ወዲህ ግን ጋዜጦች ቀናቸውን ጠብቀው ስለማይወጡና መ/ቤቱ በፈለገው ጊዜ ስለማያገኛቸው፣ ውሉን ለማቋረጥ ማሰቡን ይገልፃል፡፡ የተለያዩ ጨረታዎችን፣መስሪያ ቤቱን የተመለከቱ ዜናዎችንና አጠቃላይ መረጃዎችን በትኩሱ ማግኘት እንደሚፈልግ የተናገረው የህዝብ ግንኙነት ባለሙያው፤የሚዲያ ድርጅቶች የደንበኝነት ውል የገባንባቸውን ጋዜጦች ለምን በወቅቱ እንደማያቀርቡ ሲጠየቁ “ማተሚያ ቤት ማሽን ተበላሽቶ ነው” የሚል ተመሳሳይ ምላሽ እንደሚሰጡ ጠቁሞ “በዚህ አይነት እስከመቼ ይዘለቃል፤አሳታሚዎች በጉዳዩ ላይ ተመካክረው አንድ ነገር ላይ መድረስ አለባቸው” ሲል ምክሩን ለግሷል፡፡
የጋዜጣ ማርፈድ ችግር የቆየ ቢሆንም ከጥቂት ወራት ወዲህ ግን ተባብሷል ይላል - የካፒታል ጋዜጣ አዘጋጅ ግሩም፡፡ ማርፈዱ ደግሞ ጦሱ ብዙ ነው፡፡ “በአሁኑ ጊዜ በፊት ከምናሳትመው በአስር ፐርሰንት ቀንሷል፤ ስምንት ሺ አዝዘን ከአምስት መቶ እስከ ስምንት መቶ እንቀንሳለን” ያለው አዘጋጁ፤ ኮፒ ብቻ ሳይሆን ገፆችም እንደሚቀንሱ፣ ወደ ክፍለሃገር የሚላኩትም እንደሚቀሩ ገልጿል፡፡ “ከቀናችን ሁለት ቀን ዘግይተን ስለምንወጣም ዜና መስራት ሁሉ ትተናል” ይላል ግሩም፡፡
ለጋዜጣው ማርፈድና ማደር ምክንያቱ የብርሃንና ሰላም ማሽኖች ማርጀት ነው የሚለው የካፒታል አዘጋጅ፤ ይህም የጋዜጣውን ሽያጭ በማስተጓጎል ለከፍተኛ ኪሳራ ዳርጎታል ብሏል፡፡ “አሁን አሁን በቀናችሁ ትወጣላችሁ ወይ ስንባል፣ መልሳችን ‘የብርሃንና ሰላም ማሽን ካልተበላሸ---’ የሚል ሆኗል” ይላል አዘጋጁ፡፡
የሪፖርተር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ መላኩ ደምሴ በበኩሉ፤ የማተሚያ ቤት ችግር ከአቅም በላይ እንደሆነ ጠቁሞ፣አሁን ካለው ችግር ይልቅ የወደፊቱ እንደሚያሳስበው ይናገራል፡፡ “ሪፖርተር ጋዜጣ በሳምንት ሶስት ጊዜ ነው የሚታተመው፤ላለፉት 20 ዓመታትም የብርሃንና ሰላም ደንበኞች ሆነን ቆይተናል” ያለው ጋዜጠኛ መላኩ፤ “ሪፖርተር በዓመት እስከ 30 ሚሊዮን ብር ለማተሚያ ቤቱ  ቢያስገባም እንዲህ አይነት መጉላላትና ችግር ሲደርስብን ከአመራሩ ጀምሮ እስከ ሰራተኛው ድረስ ሊያማክሩንና የት ወደቃችሁ ሊሉን ይገባ ነበር እነሱ ግን ምንም አይነት የጥፋተኝነት ስሜት እንኳን አይሰማቸውም” ብሏል፡፡
 ሰሞኑን ብሄራዊ ፈተና እየታተመ መሆኑ እንደ ሰበብ ቢቀርብም ችግሩ ግን ከዚያም በፊት ነበረ ይላል - ጋዜጠኛ መላኩ፡፡ ብርሃንና ሰላም በተደጋጋሚ ማሽን ተሰበረ፣ ቀለም የለም፣ ኬሚካል አልቋል---በሚሉ ሰበቦች መከራ እንዳበላቸው አስታውሶ፤ አሁን እየታተመ ባለው ብሄራዊ ፈተና ሰበብ ደግሞ ለብዙ  ችግርና ኪሳራ እንደተዳረጉ ገልጿል፡፡ ጋዜጣ ባደረና በሰነበተ ቁጥር ስርጭቱ ላይ ከፍተኛ ችግር ከመፍጠርም ባሻገር፣ ባለማስታወቂያዎች በቀነ ገደብ የሚያስነግሯቸው ማስታወቂያዎች ቀናቸውን መሳትና ሌሎች  ከሞራል ጋር የተያያዙ ቀውሶች እንደሚያስከትል ዋና አዘጋጁ ተናግሯል፡፡ “እሁድ በሚወጣ ጋዜጣ ለሰኞ የስብሰባ ጥሪ ማስታወቂያ ያወጣ ድርጅት፤ጋዜጣው ማክሰኞ ሲወጣ ለምን ክፍያ ይፈፅማል?” ሲል የሚጠይቀው መላኩ፤“በተመሣሣይ መልኩ በርካታ ድርጅቶች ክፍያ ላይፈፅሙ ይችላሉ፤እናም ኪሳራው ብዙ ይሆናል” በማለት አስረድቷል፡፡
የጋዜጦች መዘግየት ጋዜጣ አዟሪዎችንም ክፉኛ እየጎዳቸው ነው፡፡ ላለፉት 12 ዓመታት በጋዜጣ አዟሪነት የሰራው ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ ጎልማሳ፤ “አሁን እንደ በፊቱ ብዙ ጋዜጦች የሉም፤ ያሉትም በቀናቸው ስለማይወጡ ገበያችን እየቀዘቀዘ ነው” ብሏል፡፡ በዚህም የተነሳ አዟሪዎች ፊታቸውን ወደ መፅሄቶች እንዳዞሩ ይናገራል፡፡ “አንዳንድ ጋዜጦች በተመላሽ አይሰጡም፤ እኛ በተመላሽ ካላስረከብን ደግሞ  ለኪሳራ እንዳረጋለን” ያለው ጋዜጣ ሻጭ፤ “ከዚህ ሁሉ ቀናቸውን አሳልፈው ሲወጡ ቁጥሩን ቀንሰን እንረከባለን፤ይሄ በገበያችን ላይ ጉዳት ቢኖረውም ብዙ ጋዜጣ ወስደን ከምንከስር መቀነሱ ይሻላል” ይላል፡፡ የጋዜጦች በቀናቸው አለመውጣት በአሳታሚዎችም ሆነ በአዟሪዎች ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ጫና እያሳደረ እንደሆነ የጠቆመው ጋዜጣ አዟሪው፤በአሁኑ ሰዓት በፊት ከሚረከበው የጋዜጣ መጠን በግማሽና ከዚያም በላይ ቀንሶ እየተረከበ መሆኑን ገልጿል፡፡
በዜድ ፕሬስ ስር የሚታተመው ሳምንታዊው ኢትዮ ቻናል ጋዜጣ በቀኑ መውጣት ባለመቻሉ ለከፍተኛ ኪሳራ እየተዳረገ መሆኑን ሳምሶን አድቨርታይዚንግ ባለቤት ሳምሶን ማሞ ተናግሯል፡፡ “በጋዜጣው ላይ ማስታወቂያ የሚያወጡት ድርጅቶች በቀኑ ካልወጣ ክፍያ አይፈፅሙም፤ ስለዚህ ኪሳራው የድርጅታችን ነው” ያለው ሳምሶን ማሞ፤ “የጋዜጣው ህልውና አደጋ ላይ በመሆኑ እንዝጋው አንዝጋው በሚለው ላይ እየተወያየን ነው” ብሏል፡፡
የብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ ተካ አባዲ ለጋዜጦች መዘግየት ሁለት ምክንያቶችን ይጠቅሳሉ፡፡ አንደኛ፤ጋዜጦቹን የሚያትሙት ማሽኖች የቆዩ ስለሆነ አቅማቸው እየወረደ ነው፤ አቅማቸውን ለመገንባት መለዋወጫ ለመግዛት ቢጠይቁም መሳሪያዎቹን ያመረተው ፋብሪካ ስራ በማቆሙ መለዋወጫዎቹን ማግኘት አልቻልንም ብለዋል። ሁለተኛው ምክንያት የብሔራዊ ፈተና ሕትመት መጀመር እንደሆነ አቶ ተካ ተናግረዋል፡፡ ማተሚያ ቤቱ በደንበኞች ቅሬታ ላይ ሥር-ነቀል ለውጥ ለማምጣት ከአንድ ዓመት በፊት “ክሪስ ግሩፕ” በተባለ ኩባንያ አንድ ጥናት ማስጠናቱን ጠቅሰው፤ አሁን መንግሥት በፈቀደላቸው 558 ሚሊዮን ብር ጥናቱን ተግባራዊ ማድረግ እንደ ጀመሩ ገልፀዋል፡፡ ከጃፓን የገዟቸው ሁለት ኦፍሴት ማሽኖች እስከ ግንቦት ድረስ ይገባሉ፡፡ አንዱ ለጋዜጣ ሕትመት፣ ሌላኛው ለመጻሕፍት ህትመት ብቻ ዲዛይን የተደረጉ ናቸው፡፡ በአንድ ጊዜ አራት ቀለም የሚያትመው መሳሪያም ገብቶ እየተተከለ ነው፡፡ ሌሎች በጥናቱ የተካተቱ የመፍትሔ ሀሳቦች ትግበራም በሂደት ላይ ነው ብለዋል አቶ አባይ፡፡
 የአታሚዎች ማህበር ፕሬዚዳንት እንደሆኑ የገለፁት ሥራ አስኪያጁ፤አሁን መንግሥት በፈቀደው በጀት ማተሚያ ድርጅቱን በማጠናከር ያሉትን ጥቂት ጋዜጦች በጥራትና በብቃት ለማተም መዘጋጀታቸውንና ተጨማሪ 20 እና 30 ጋዜጦች ወደ ብርሃንና ሰላም መጥተው እንዲታተሙ ለማድረግ ፍላጎት እንዳላቸው ገልፀዋል፡፡ አሁንም በተፈቀደው በጀት የማተሚያ ማሽኖች ተገዝተው እየገቡ በመሆናቸው መጪው ጊዜ ለህትመቱ ኢንዱስትሪ ብሩህ እንደሚሆን ይናገራሉ፡፡
 የብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት ሠራተኞች ማህበር ተወካይ በበኩላቸው፤ የጋዜጦች መዘግየት እውነት መሆኑን አምነው፤ አሳታሚዎች ዘንድም ችግር እንዳለ ይናገራሉ፡፡ “ማተሚያ መሳሪያው አርጅቶ ጥርሱ በመበላሸቱ መዘግየት ይፈጥራል፤ ሌላው ምክንያት ደግሞ አሳታሚዎች ጋ ያለ ችግር ነው፤ በፍላሽ ወይም በወረቀት የሚያመጡት ጽሑፍ፣ የጥራት ወይም ሌላ ችግር ኖሮት አስተካክላችሁ አምጡ ስንላቸው በጊዜ አያቀርቡም፣ በዚህም ይዘገያል፡፡ ጋዜጦች ተደራርበው መምጣታቸውም እንዲሁ ለመዘግየት ምክንያት ነው ይሆናል” ብለዋል፡፡
አቶ ተካ እንደሚሉት ለወደፊት ያሰቡት ትልቁና ዋንኛው እቅድ ከደንበኞች ጋር የሚገቡት የተጠያቂነት ቻርተር ነው፡፡ “ለምሳሌ አዲስ አድማስ ወይም ሌላ አሳታሚ ድርጅት፣ ጋዜጣው የታተመበትን ዋጋ ባይከፍል ድርጅቱን ከስሰን የሰራንበትን ዋጋ እናስከፍላለን፡፡ እኛ ህትመት ብናዘገይ፣ ጋዜጣውን ወይም መጽሔቱን ከሁለትና ከሶስት ቀን በኋላ ብናትም፣ ጥራት ብናጓድል፣ እስካሁን በነበረው አሰራር በተለያዩ ምክንያቶች አንጠየቅም፣ አንከሰስም፡፡ በቢዝነስ ዓለም አንዱ የሚጠየቅበትና ሌላ የማይጠየቅበት አሰራር ትክክል አይደለም፡፡ ለምሳሌ እናንተ ጋዜጣ ላይ የወጣ ሰው ፎቶግራፍ ቢበላሽ፣ ግለሰቡ እናንተን ይጠይቃል፣ እናንተ ደግሞ በሶስተኛ ወገን ተጠያቂነት እኛን መጠየቅ አለባችሁ፡፡ ሁሉም ወገን ባጠፋው ነገር ወይም በሰራው ስህተት መጠየቅ አለበት፡፡ ቃል የምንገባበት የተጠያቂነት ውል (ቻርተር) አዘጋጅተናል፡፡ ይህ የአመራሩ ውሳኔ ብቻ አይደለም፡፡ የሰራተኛ ማህበሩን “ቃላችንን ባናከብር፣ ህትመት ብናገዘይ፣ ጥራት ብናጓድል፣… ደንበኞቻችን እንዲጠይቁን የሚያደርግ ውል ልንገባ ነው” ብለን ነገርናቸው፡፡ እነሱ ደግሞ ለሰራተኛው ነገሩ፡፡ የህልውና ጉዳይ ስለሆነ በአንድ ድምፅ ነው የተቀበሉት” በማለት ገልጸዋል፡፡
 ከዚህ ቀደም ብርሃንና ሰላም ከአሳታሚዎች ጋር ውል እንፈራረም ሲል መጠየቁን ያስታወሱ አንድ የቀድሞ ጋዜጣ አሳታሚ፤ “ውሉ ጋዜጦች የሚያስጠይቁ ፅሁፎች ይዘው ሲያመጡ፣ብርሃንና ሰላም አላትምም የማለት መብት አለው” የሚል ይዘት እንደነበረውና አሳታሚዎች ሳይቀበሉት እንደቀሩ ተናግረዋል። “በፕሬስ ህግ መሰረት የሚያስጠይቅ ፅሁፍ ቢፃፍ የመጀመሪያ ተጠያቂ ዋና አዘጋጁ፣ ዋና አዘጋጁ ከጠፋ ኩባንያውና አሳታሚው፤ እነዚህ አካላት ከጠፉ ደግሞ አታሚ ድርጅቱ ተጠያቂ ይሆናል” ያሉት አሳታሚው፤ እነዚህን ሁሉ ዘሎ ለሚመጣ ተጠያቂነት ነው ብርሃንና ሰላም አላትምም ያለው ብለዋል፡፡ “ብርሃንና ሰላም አላትምም ሲል የትም መሄጃ አማራጭ አልነበረንም፤ ያም ሆኖ ውሉን አልፈረምንም፣ ከዚያን ጊዜ ወዲህ ነው ጋዜጦች ማተሚያ ቤት እያረፈዱና እያደሩ መውጣት የጀመሩት” ሲሉ ይወቅሳሉ፡፡
አቶ ተካ ግን ዋናው ችግር የአቅም ማነስ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ “ጋዜጦች አንዳንዴ አርፍደው ይወጣሉ፣ አንድና ሁለት ቀን የሚዘገዩበትም ጊዜ አለ፡፡ በዚህ ጊዜ ደንበኞቻችን ’አዲስ ዘመን የመንግሥት ስለሆነ አስቀደማችሁት፣እኛ የግል ስለሆንን አሳደራችሁ፣…’ ይሉናል፡፡ እውነቱን ለመናገር ይኼ የወገንተኝነት ጉዳይ አይደለም፤ የአቅም ማነስ፣ የማተሚያ መሳሪያዎች እርጅና ነው፡፡ ይህ ችግር በቅርቡ ስለሚፈታና ስለሚስተካከል የደንበኞቻችን እሮሮና ቅሬታ ይወገዳል።” ብለዋል፡፡
ሰባት ዓመት በህትመት ላይ የቆየ ጋዜጣቸው በማተሚያ ቤቱ ችግር እንደቆመባቸው የሚናገሩት የቀድሞ አሳታሚ ግን በአቶ ተካ አባባል አይስማሙም፡፡ “ማተሚያ ቤት ገብተን የእኛ ጋዜጣ ህትመት ተጀምሮ ቢሆን እንኳን አዲስ ዘመን ከመጣ የእኛ ተቋርጦ እሱ ይታተማል” በማለት ያፈጠጠ ወገንተኝነት እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡
ማተሚያ ቤቱ በቅርቡ በብዙ ሚሊዮን ብሮች ዘመናዊ ማሽን ከስዊድን ማስመጣቱን የገለፀው የሪፖርተር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ መላኩ ደምሴ፤ለማሽኑ ተስማሚ እውቀትና ስልጠና የወሰዱ ሰራተኞች ስለሌሉ ማሽኑ በአግባቡ መስራት እንዳልቻለ ተናግሯል፡፡ “ድርጅቱ ይህን የሚያህል ዘመናዊ ማሽን ሲያስመጣ ማሽኑን በአግባቡ የሚያንቀሳቅሱ ሰራተኞች ሰልጥነው እንዲመጡ አለማድረጉ ለዘርፉ ትኩረት አለመስጠቱን ያመለክታል” ሲል ወቅሷል፡፡ ከስዊዲን የመጣው ማሽን ትክክለኛ ባለሙያ ቢመደብለት አሁን ያለውን የአሳታሚዎች ችግር መፍታት እንደሚችልም ጨምሮ ገልጿል፡፡
 የማንኛውም መ/ቤት የመጨረሻ ግብ፣ የተማረና የሰለጠነ የሰው ኃይል ሀብት ነው - ይላሉ አቶ ተካ፡፡ “የዘመናዊ መሳሪያ ባለቤት መሆን በራሱ የመጨረሻ ግብ አይደለም፡፡ የተማረ የሰው ኃይል ለማፍራት የህትመት ኢንዱስትሪ አካዳሚ ለመክፈት ባለ 7 ምድር ቤትና 6 ፎቅ ህንፃ ለመገንባት ተወስኖና በጀት ተመድቦ፣ ህንፃው የሚሰራበትን ቦታ ማስተካከል ተጀምሯል፡፡ አዳዲስ ለተገዙት ዘመናዊ መሳሪያዎች፣ ሠራተኞች ውጭ አገር ልከን በአጫጭር ኮርሶች እናሰለጥናለን፡፡” ብለዋል፡፡
 “አሁን ያለው የማተሚያ ቤት ችግር ተስፋ አስቆራጭ ነው” የሚለው የኢትዮ ቻናል ባለቤት ጋዜጠኛ  ሳምሶን፤ ብርሃንና ሰላምም ሆነ መንግስት ለችግሩ አፋጣኝ መፍትሔ ካላመጡ በህትመት የምንቆይበት ተስፋ የለም ብሏል፡፡  
የካፒታል ጋዜጣ አዘጋጅ ግሩም እንደሚለው፤ “ጋዜጣችን ሙሉ በሙሉ በማተሚያ ቤቱ ችግር ዘግይቶ እየወጣ ለኪሳራ ስንዳረግ ዝም መባል የለበትም፤ ማተሚያ ቤቱ ሲሆን 100 ፐርሰንት ካልሆነ 50 ፐርሰንት ኪሳራችንን ሊጋራን ይገባል”
ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት መጋቢት 9 ቀን 2006 ዓ.ም ከጋዜጣ አሳታሚ ድርጅቶች ጋር ለመወያየትና የተጠያቂነት ውል ለመፈረም ጥሪ አድርጓል፡፡

መጽሐፉ ለአቡነ ማትያስና ለጠ/ሚ ኃይለማርያም እንዲደርሳቸው ተደርጓል
ደብዳቤው ለእስራኤሉ ጠ/ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታናሁ እና ለተመድ ተልኳል

       ከተፃፈ ከ2 ሺህ ዓመታት በላይ አስቆጥሯል የተባለውንና ስለ ቅዱስ ኤልያስ መምጣት ምስጢር የሚተነትነውን መጽሐፍ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ተቀብላ ወደተለያዩ ቋንቋዎች በማስተርጎም ምዕመናኖችን እንድታስተምር፣ “ማህበረ ሥላሴ ዘደቂቀ ኤልያስ” ለቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በጻፈው ደብዳቤ ጠየቀ፡፡
ማህበሩ፤የመጽሐፉን ኮፒዎች ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሣለኝ እና ለብፁዕ አቡነ ማትያስ  ህዝቡን እንዲያስተምሩበት ከሚያሳስብ ደብዳቤ ጋር መላኩን አስታውቋል፡፡
አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን አባል የሆነችበት ማህበረ ሥላሴ፤“ቅድስት ቤተ-ክርስቲያን ለሁለት ሺህ ዘመን ስትጠብቀው የቆየችውን ምስጢራዊ መጽሐፍ በአደራ የመረከብና ለዓለም ሁሉ የማሳወቅ ፅኑ ኃላፊነትን ይመለከታል” በሚል ርዕስ ለፓትርያርኩ፣ በግልባጭ ደግሞ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ እንዲሁም ለእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔትናሁ እና ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት በፃፈው  ደብዳቤ “ማህፈድ ብርህት ዘዲዮስቆሮስ አንበሳ” በሚል ርዕስ በግዕዝ ቋንቋ የተፃፈውን መጽሀፍ፣ የቤተ-ክርስቲያኗ ሊቃውንት ተቀብለው ምእመናኑን ስለ ቅዱስ ኤልያስ እና ትክክለኛይቱ ሰንበት እንዲያስተምሩበት አሳስቧል፡፡
ደብዳቤው ለእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር የተላከው ኢትዮጵያና እስራኤል በመንፈሣዊ አሰራር አንድ ስለሚሆኑበት ሁኔታ ለማመልከት ነው ያሉት የማህበሩ አመራሮች፤ለተባበሩት መንግሥታት የተላከውም መልእክቱ ለዓለም ሁሉ እንዲዳረስ ስለሚፈለግ ነው ብለዋል፡፡
ከ2 ሺህ ዓመታት በፊት እንደተፃፈ የሚነገርለት መጽሐፉ፤ ስለ ቀዳሚት ሰንበት ምንነትና ዘለዓለማዊነት በግልፅ እንደሚያብራራ እንዲሁም የኢትዮጵያና የእስራኤልን አንድነትና ትንሳኤ ምስጢር ተንትኖ እንደሚያስረዳ ተጠቁሟል፡፡
ማህበሩ በላከው መልዕክት፣ ቅዱስ ኤልያስ ከብሄረ ህያዋን ይዞት የመጣውን መጽሀፍ፣ የቤተ-ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት እንዲመረምሩት፣ በተለያዩ ቋንቋዎች እንዲተረጎምና እንዲታተም፣ ምዕመናንም እንዲያነቡት የማድረግ ግዴታ ፓትርያርኩ እንዳለባቸው ያሳስባል፡፡ “ይህ ሳይሆን በእንቢተኝነትና በቸልታ ለዘመናት በተስፋ የተጠበቀውን ይህን መጽሀፍ እንዳይቀርብ ቢያደርጉ፣ ከብሄረ ህያዋን የመጣው ቀናኢ ነቢይ ዓለምን ሁሉ እየገሰፀ ባለበት ኃያል፣ ስልጣኑ ፅኑ ፈራጅነቱና ቁጣው የሚፈርድ መሆኑን አረጋግጠን እንነግርዎታለን” ብሏል፡፡ “ለቤተ-ክርስቲያኒቱ ሲኖዶስ እና ካህናት ጥፋትና የመጨረሻው ውድቀት ነው” ሲልም ለመፅሃፉ ትኩረት እንዲሰጥ ማህበሩ  አበክሮ አሳስቧል፡፡
በጉዳዩ ዙሪያ የፓትርያርኩን ጽ/ቤት እና የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጽ/ቤት በስልክ አግኝተን ለማነጋገር ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡


Published in ዜና

ማርች 8 አለማቀፍ የሴቶች ቀንን ምክንያት በማድረግ በተካሄደው የሴቶች የጎዳና ላይ ሩጫ ‹‹አንዳንድ ያልተገቡ ድርጊቶች ፈፅማችኋል›› በሚል በፖሊስ ቁጥጥር ሥር የዋሉ አስር ከፍተኛ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አባላት ትላንት ፍ/ቤት ቀርበው ፖሊስ አራት ተጨማሪ የምርመራ ቀናት ጠየቀባቸው፡፡
በቁጥጥር ስር የዋሉት 7 ሴቶችና 3 ወንዶች የፓርቲው አባላት በጎዳና ላይ ሩጫ ‹‹አንዷለም ይፈታ፣ ርዕዮት ትፈታ፣ ውሃ ናፈቀን፣ መብራት ናፈቀን›› የሚሉ መፈክሮችን ሲያሰሙ ነበር ተብሏል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ በከፍተኛ የአመራር ቦታ ላይ ያሉና ቋሚ አድራሻ ያላቸው እንደሆኑ በመግለፅ በዋስ እንዲፈቱ ቢጠይቁም ፖሊስ በበኩሉ፤ ወንጀሉ ውስብስብ በመሆኑ አራት ተጨማሪ ቀናት የምርመራ ጊዜ ያስፈልገኛል ሲል አመልክቷል፡፡
ፍ/ቤቱም የተጠርጣሪዎቹን የዋስትና መብት በመከልከል ለትናንትና ቀጠሮ ሰጥቶ ነበር፡፡ ትላንት ፍርድ ቤት የቀረቡት ተጠርጣሪዎች ላይ ፖሊስ ተጨማሪ አራት ቀን ምርመራ ጊዜ ጠይቆ ፍ/ቤቱም ለመጭው ማክሰኞ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

Published in ዜና

ነገ የሦስት ወር ንቅናቄውን በአዲስ አበባ ይጀምራል

      ከመድረክ ጋር ያለውን ጥምረት አቋርጦ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር የውህደት ድርድር የጀመረው አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ፤በመጪው ዓመት ምርጫ የሚሳተፈው የምርጫው አስፈፃሚ አካላት ነፃና ገለልተኛ መሆናቸው ከተረጋገጠ ብቻ እንደሆነ  ሊቀመንበሩ ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው ገለፁ፡፡
በ97 ምርጫ ቅንጅት የነበረውን ጥንካሬ ፓርቲያቸው መድገም እንደሚፈልግ የገለፁት ኢ/ር ግዛቸው፤ ህዝቡ ብሶት ላይ ስለሆነ በምርጫው ተቃዋሚዎች በቀላሉ ሊያሸንፉ እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡ ፓርቲያቸው ወደ ምርጫው የሚገባው ግን ለምርጫው ነፃና ፍትሃዊ መሆን አስፈላጊ የሚባሉት ገለልተኛ የምርጫ ቦርድ፣ ሚዲያ እና የፍትህ ተቋማት መኖራቸውን ካረጋገጠ በኋላ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ “ይህ ጥያቄያችን ከተመለሰ በምርጫው በእርግጠኝነት እናሸንፋለን” ብለዋል የፓርቲው መሪ፡፡
ፓርቲያቸው ከመድረክ ጋር ስላለው ግንኙነት የተጠየቁት ኢ/ር ግዛቸው፤ አንድነት ከቢሮ እና ከመግለጫ ፖለቲካ ተላቆ ትግሉን ወደ ህዝብ ለማውረድ  ያደረገው እንቅስቃሴ የመድረክ አመራሮችን እንዳስኮረፈና እገዳው እንደተላለፈ ጠቅሰው “እገዳው ትክክል አይደለም፤ አንሱትና ባቀረብነው የውህደት ጥያቄ መሰረት አብረን እንስራ ብለናቸዋል” ብለዋል፡፡
“መድረክ ከአንድነት የተሻለ ጥንካሬ እንደሌለው ገምግመናል” ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ውህደቱን አንፈልግም ቢሉም እንኳን በሚያግባቡን ጉዳዮች ላይ በቅንነት አብረን ልንሰራ እንደምንችል ነግረናቸዋል ብለዋል፡፡
ከእዚህ በኋላ አንድነት በቀጥታ ውህደት ከመፈፀም ውጪ ከየትኛውም ፓርቲ ጋር ግንባርና ቅንጅት የመፍጠር ፍላጎት እንደሌለውም ኢ/ር ግዛቸው ጨምረው ገልፀዋል፡፡
ፓርቲው በነገው እለት “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” ሁለተኛ ዙር ንቅናቄ በአዲስ አበባ የሚጀምር ሲሆን  አጀንዳውም መሬት የግል እንዲሆን የሚጠይቅ ነው ተብሏል፡፡ ለ3 ወር ይዘልቃል የተባለውን ይሄን ንቅናቄ በተመለከተ የተጠየቁት ኢ/ር ግዛቸው፤“በአንድነት ፕሮግራም ውስጥ ከመንግሥት ይዞታና ከአንዳንድ ተቋማት ይዞታ በስተቀር መሬት የግል መሆን አለበት በሚል በግልፅ አስቀምጠናል፡፡ ይህን መነሻ አድርገን በመሬት ጉዳይ ላይ ህዝብ ተወያይቶ የራሱን አቋም የሚይዝበት ትልቅ ንቅናቄ አዘጋጅተናል” ሲሉ አስረድተዋል፡፡
 አሁን ያለው የመሬት ፖሊሲ ለኑሮ ውድነቱ መባባስ አስተዋፅኦ አበርክቷል ያሉት ኢ/ር ግዛቸው፤ “የኑሮ ውድነቱ ካለን የመሬት ሃብት ተጠቃሚ ያለመሆናችን ውጤት ስለሆነ፣ ጥያቄያችን የኑሮ ውድነት አጀንዳንም በበቂ ሁኔታ የያዘ ነው” ብለዋል፡፡ መንግስት በበኩሉ፤ መሬት የህዝብና የመንግስት ነው የሚል ፖሊሲ እንደሚያራምድ ይታወቃል፡፡
(ከአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበሩ ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው ጋር የተደረገው ቃለምልልስ ሙሉ ቃል በገፅ 5 ላይ ያገኙታል፡፡)


Published in ዜና

         በተለያዩ ወንጀሎች ፍርድ ተሰጥቶባቸው በማረሚያ ቤት ለሚገኙ የህግ ታራሚዎች የሚደረግ ይቅርታ አሰጣጥን የሚወስንና በቀድሞ አዋጅ ላይ ማሻሻያዎች የሚያደርግ ረቂቅ አዋጅ ወጣ፡፡ ረቂቅ አዋጁ በይቅርታ አሰጣጡ ላይ በሚኖረው የፕሬዚዳንቱ ሚና ላይ ማሻሻያዎችን አድርጓል፡፡ ሰሞኑን ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበው ይኸው ረቂቅ አዋጅ፤ በ1996 ዓ.ም የወጣውን የይቅርታ ስነ-ስርዓት ለማሻሻልና አዋጁ ያሉበትን ክፍተቶች ለማስተካከል ታስቦ እንደተዘጋጀ ተገልጿል፡፡
በቀድሞው አዋጅ፤የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ለታራሚዎች ይቅርታ የመስጠት ሥልጣን እንዳላቸው የተደነገገ ሲሆን አንቀፁ መሻሻያ ተደርጎበት የይቅርታ ጥያቄዎችን በመመርመር፣ ለፕሬዚዳንቱ የውሳኔ ሃሳቡን በማቅረብ የሚያጸድቀው የይቅርታ ቦርዱ እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ ለፕሬዚዳንቱ የሚቀርቡላቸው ይቅርታ ሊደረግላቸው የሚገቡ ሰዎች ዝርዝር ብቻ እንደሆነም ረቂቅ አዋጁ አመልክቷል፡፡
የፕሬዚዳንቱ ይቅርታን የመሰረዝ ስልጣን፣ በአዲሱ ረቂቅ አዋጅ ለይቅርታ ቦርድ የተሰጠ ሲሆን የይቅርታ ቦርዱ የመጨረሻ ውሳኔ በመስጠት፣ይቅርታን የመሰረዝ ስልጣንና ተግባር እንዳለው ረቂቅ አዋጁ አመላክቷል፡፡
በቀድሞው አዋጅ፤አንድ ታራሚ የይቅርታ ጥያቄ አቅርቦ ይቅርታ ከተደረገለት ግብረ አበር ወይም አባሪ የሆነው ታራሚ፣ይቅርታ እንደሚያገኝ የተደነገገ ቢሆንም ይህ አሰራር በአዲሱ ረቂቅ አዋጅ ተቀባይነት የለውም፡፡
ረቂቅ አዋጁ ይቅርታን ሊያስከለክሉ የሚችሉ ወይንም የይቅርታ ጥያቄ ሊቀርብባቸው የማይችሉ ብሎ በዝርዝር ከጠቀሳቸው ወንጀሎች መካከል ሙስና፣ ሽብርተኝነት፣ ህገወጥ የጦር መሳሪያና የሰዎች ዝውውር፣ በመሰረተ ልማት አውታር ላይ የሚፈፀም ወንጀል፣ የሃሰት ገንዘብ መስራት፣ ማዘዋወር፣ የአደገኛ እፅ ዝውውር፣ የጠለፋና አስገድዶ መድፈር ወንጀል፣ ግብረ ሰዶማዊነትና ህገወጥ የቅርሶች ዝውውር ይገኙባቸዋል፡፡
የይቅርታ ጥያቄዎችን የሚመረምርና የውሳኔ ሃሳቦችን ለፕሬዚዳንቱ በማቅረብ የሚያሰወስነው ከፍትህ፣ ከጤና ጥበቃ፣ ከሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ፣ ከፌዴራል ጉዳዮች፣ የሴቶች ህፃናትና ወጣቶች፣ ከመከላከያ ሚኒስቴር መ/ቤቶች፣ ከፌደራል ፖሊስ ኮሚሽንና ከፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር የሚዋቀር የይቅርታ ቦርድ እንደሆነም በረቂቅ አዋጁ ላይ ተገልጿል፡፡

Published in ዜና

 ከቻይና በተገኘ የ4.3 ቢ. ብር ብድር የማስፋፊያ ሥራ ይከናወናል  

የአዲስ አበባው ቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት፤መንገደኞችን የማስተናገድ አቅሙ እየተጣበበ በመምጣቱ በአሁኑ ወቅት ያለውን የትራፊክ ፍሰት በአግባቡ ማስተናገድ ወደማይችልበት ደረጃ ላይ እየደረሰ መሆኑ ተገለፀ፡፡ በህንፃው ውስጥ ያለው ከፍተኛ የመጣበብ ችግር፤ በአየር መንገዱ የአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ጫና በመፍጠር የአገልግሎት ጥራቱን እያወረደው ነው ተብሏል፡፡
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰሞኑን ባካሄደው መደበኛ ስብሰባው ላይ በቀረበ የብድር መግለጫ ሪፖርት ላይ እንደተገለጸው፤ አየር መንገዱ ያለበት የመጨናነቅ ችግር አስቸኳይ መፍትሔ ካላገኘ የአየር መንገዱ ደረጃ ዝቅ ብሎ ተወዳዳሪነቱን እንዳያጣ ያሰጋል፡፡ አየር መንገዱ በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ካላቸው የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት መመዘኛዎች አንፃር ሲታይ ጥራቱ ዝቅተኛ የሆነ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን የጠቆመው ሪፖርቱ፤ከጊዜ ወደ ጊዜ የአገልግሎት ጥራቱ እየቀነሰ እንደመጣም  ተገልጿል፡፡
ደረጃው ከዕለት ወደ ዕለት እየወረደ የመጣውን የአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት አገልግሎት አሰጣጥ ለማሻሻል እና በቀጣይነት ተመራጭ ኤርፖርት ለማድረግ ፕሮጀክት መነደፉን የገለፀው ሪፖርቱ፤ ከቻይና ኤክስፖርት ኢምፖርት ባንክ ለፕሮጀክቱ ማስፈፀሚያ 225 ሚሊዮን ዶላር (ከ4.3 ቢሊዮን ብር በላይ) ብድር መገኘቱን አመልክቷል፡፡ ብድሩ በዓመት የ2% ወለድ የሚከፈልበት ሲሆን  በሃያ ዓመት ጊዜ ውስጥ ተከፍሎ የሚጠናቀቅ እንደሆነም ተገልጿል፡፡

Published in ዜና

          የ38 አመቱ ኢትዮጵያዊ ዶክተር ፍሰሃ ኡንዱቼ በካናዳ የመሰረተ ልማትና የትራንስፖርት ሚኒስቴር የማኒቶባ ግዛት የአየር ንብረትና የጎርፍ አደጋ ትንበያ ዳይሬክተር ሆነው መመረጣቸውን ዊኒፒንግ ፍሪ ፕሬስ ዘገበ፡፡
የካናዳ የመሰረተ ልማትና የትራንስፖርት ሚኒስትር ስቲቭ አሽተን ዶክተሩን ለመገናኛ ብዙሃን ለማስተዋወቅ በተዘጋጀ ስነስርዓት ላይ ተገኝተው እንደተናገሩት፣ ከተለያዩ አገራት የተውጣጡ በርካታ ባለሙያዎች የተሳተፉበትን ከፍተኛ ውድድር በማሸነፍ ለማኒቶባ ግዛትየአየር ንብረትና የጎርፍ አደጋ ዳይሬክተር ለመሆን የተመረጡት ዶክተር ፍሰሃ፣ ላለፉት 15 አመታት በሃይድሮሎጂና ከጎርፍ አደጋ ጋር በተያያዙ ጉዳዮች በአሜሪካና በተለያዩ የአውሮፓ አገራት የካበተ የስራ ልምድ አላቸው፡፡
ላለፉት አምስት አመታት የግዛቷ የውሃ ቁጥጥር ስርዓቶች ዕቅድ ከፍተኛ መሃንዲስ ሆነው ያገለገሉት ዶክተር ፍሰሃ፣ ከዚያ ቀደምም ኤኢኮም በተባለ አለማቀፍ የምህንድስና አገልግሎቶች ኩባንያ ውስጥ የውሃ ሃብቶች መሃንዲስ ሆነው ማገልገላቸው ተነግሯል፡፡ ኒዘርላንድ ውስጥ ከሚገኘው ኢንተርናሽናል ሃይድሮሊክ ኢንጂነሪንግ ኢንስቲቲዩት በሲቪል ምህንድስና የሁለተኛ ዲግሪያቸውን የተቀበሉት ዶክትር ፍሰሃ፣ በኖርዌጂያን ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ሳይንስ ኤንድ ቴክኖሎጂ ሌሎች የምርምር ጥናቶችን እንደሰሩ ተጠቁሟል፡፡
ከማኒቶባ ዩኒቨርሲቲ በውሃ ሃብቶች የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ከተቀበሉ በኋላም፣ በተለያዩ ተቋማት ውስጥ ከጎርፍ አደጋ ትንበያና ከአደጋ ቁጥጥር ጋር በተያያዙ ጉዳዮች በውሃ ሃብቶች መሃንዲስነትና በመምህርነት አገልግለዋል፡፡በወቅቱ ከጋዜጠኞች ጥያቄ የቀረበላቸው ዶክትር ፍሰሃ፣ በውሃው ዘርፍ የጀመሩትን ጥናት አጠናክረው ለመቀጠል የሚያስችሏቸውን የጎርፍ አደጋዎች የሚበዙባቸው አካባቢዎችና በጎርፍ አደጋ ትንበያ ላይ ልዩ ትኩረት አድርገው የሚሰሩ ዩኒቨርሲቲዎች ሲያጠኑ እንደቆዩና ማኒቶባ ግዛት ለዚህ ተመራጭ መሆኗን በማረጋገጥ ወደዚያው ለመሄድ መወሰናቸውን ተናግረዋል፡፡
ዶክተር ፍሰሃ ባለትዳርና የሁለት ልጆች አባት ናቸው፡፡




Published in ዜና

          የበርካታ ሀገራትን ፖለቲካዊና፣ ኢኮኖሚያዊ ውህደት በተመለከተ አለማችን በየትኛውም ክፍሏ ቢሆን ከአውሮፓ ህብረት በተሻለ የተሳካ የሀገራት ውህደት ነው በሚል ልትጠቅሰው የምትችለው ነገር አንድም እንኳ የላትም፡፡ ይህ እውነትም ትክክልም ነገር ነው፡፡
የዛሬ ሀምሳ ሰባት አመት የፈረንሳይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በነበሩት ሮበርት ሹማን ሀሳብ አመንጭነት፣ በስድስት የምዕራብ አውሮፓ አገራት የተመሠረተው የአውሮፓ ህብረት፤ ዛሬ ሀያ ስምንት ሀገራትን በአባልነት አቅፎ ይዟል፡፡ ይህ እድሜ ጠገብ የሀገራት ህብረት፤ የውህደት አድማሱን የማስፋት ብርቱ እንቅስቃሴው ዛሬም ድረስ ለአፍታ እንኳ አልተገታም፡፡ ከዛሬ አራት አመት በፊት የወጠነውን ህብረቱን፤ ወደ ምስራቅ አውሮፓ የማስፋት እቅድ እውን ለማድረግ፣ ባለፈው አመት ሰኔ ላይ ክሮኤሻን ሀያ ስምንተኛ አባል አድርጐ በመቀበል ጀምሯል፡፡
የአውሮፓ ህብረት አድማሱን ወደ ምስራቅ አውሮፓ በማስፋት ሊቀዳጀው ካሰባቸው ፖለቲካዊ ግቦች አንዱና ዋነኛው በምስራቅ አውሮፓ ራሺያ ያላትን ተጽዕኖ በመግታት፣ በምትኩ የህብረቱን የተጽዕኖ አድማስ ይበልጥ እንዲሰፋ ማድረግ ነው፡፡ ለዚህ ግብ መሳካት ወሳኝ ሚና ይጫወታሉ ተብለው ለአባልነት በግንባር ቀደም እጩነት ከታሰቡት የምስራቅ አውሮፓ ሀገራት መካከል ደግሞ ዋነኛዋ ሀገር ዩክሬይን ናት፡፡
በ1990ዎቹ መጀመሪያ ላይ ሶቪየት ህብረት ስትፈራርስና የቀዝቃዛው ጦርነት ፍፃሜውን ሲያገኝ፣ ከእንግዲህ ወዲህ የራሺያ እጣ ፈንታ የድሮ የገናናነት ታሪኳን ወግ እየጠረቀች በትዝታ መኖር ብቻ ነው በሚል ከአሜሪካ በስተቀር አብዛኞቹ ሀገራት በእርግጠኝነት ገምተው ነበር። አሜሪካ ግን ምንም እንኳ ዋነኛ የርዕዮተዓለም ባላንጣዋ የነበረችው ሶቪየት ህብረት በመፈራረሷ ጓዝ ቀለለልኝ ብላ ደስ ቢላትም፣ የራሺያን ነገር ግን መቼውንም ጊዜ ቢሆን ችላ ብላ ትታው አታውቅም። ለአሜሪካ ራሺያ ማለት የተኛ ድብ ማለት ናት፡፡ መቼ ነቅታ እጅግ ስለታም ጥፍሮቿን እንደምታነሳ ጨርሶ የማትታወቅ፡፡
እናም የራሺያን ነገረ ስራ ሁሉ ነቅቶ መቆጣጠርና፣ የተጽዕኖ አድማሷን እንዳታሰፋ ማድረግ ለአሜሪካ የትናንትም ሆነ የዛሬ የብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቂያ ዋናና የቅድሚያ አጀንዳዋ ነው። ለዚህ አጀንዳዋ መሳካት ደግሞ ዩክሬንን ከራሺያ ጉያ መንጠቅ መቻልን የመሰለ ድል የላትም፡፡ ፊቱኑ ጀምሮ ቅጥ ያለው ፍቅር ኖሮአት ከማያውቀው የአውሮፓ ህብረት ጋር በአዲስ ፍቅር መሞዳሞድ ጀምረው፣ አንድ ቦላሌ ለሁለት ካለበስን ብለው፣ አሁን ለያዥ ለገራዥ ያስቸገሩበት ዋናው ምክንያትም ይሄው ነው፡፡
የተኛች ድብ ናት ለተባለችው ራሺያና ለፕሬዚዳንቷ የዩክሬን ጉዳይ መቼውንም ጊዜ ቢሆን የተራ ጉርብትና ጉዳይ ሆኖ አያውቅም፡፡ ለራሺያ የዩክሬን ጉዳይ የአባት ሀገር ብሔራዊ ጥቅምና ደህንነት ጉዳይ ነው፡፡ ቆፍጣናው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን የቀድሞ ሶቪየት ህብረት አባል ሀገራትን በተለይም ዩክሬንን ማዕከል አድርጐ ያካተተ፣ ዩሮኤሽያቲክ ህብረት ለመመስረት በሙሉ ሀይላቸው እየተንቀሳቀሱ የሚገኙበት ዋነኛ ምክንያትም የአባት ሀገር ራሺያን ብሔራዊ ጥቅምና ደህንነት በማስጠበቅና የተጽዕኖ ምህዳሩን በማስፋት፣ የቀድሞ ክብርና ዝና ለማስመለስ ነው። ስለዚህ ዘመናትን የተሻገረ የታሪክ፣ የባህልና የሰው ለሰው ግንኙነት ጥልቅ ትስስር ያላት ዋነኛ ጐረቤቷና አጋሯ ዩክሬን፤ በአውሮፓ ህብረትና በአሜሪካ ተጠለፈች ማለት ለፕሬዚዳንት ፑቲንና ለሀገራቸው የጦር ሀይል በቁም የመሞት ያህል ነው፡፡
ዩክሬናውያንም ቢሆኑ የወደፊቱንም አለም አቀፍ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ግንኙነታቸውን በተመለከተ ጠረጴዛቸው ላይ የቀረበላቸው ምርጫ፣ ከአውሮፓ ህብረትና ከአሜሪካ ጋር አሊያም ከራሺያ ጋር መግጠም ብቻ መሆኑን በሚገባ ተረድተውት ነበር፡፡ የህይወት መስዋዕትነት እስከ መክፈል ድረስ ሁለት ጐራ ለይተው አምባጓሮ ያስነሱትም ለዚህ ነበር፡፡
ዩክሬናውያን የማታ ማታ ምርጫቸው ከአውሮፓ ህብረትና ከአሜሪካ ጋር መወገን ሆነ፡፡ ቀላል የማይባል የህይወት፣ የአካልና የንብረት መስዋዕትነት በመክፈል አፍቃሬ ራሺያ የነበሩትን ድሎት አፍቃሪና ቅንጡውን ፕሬዚዳንታቸውን ቪክሮ ያኑኮቪችን፣ የስልጣን ወንበራቸውን አስጥለው ነፍሴ አውጭኝ ብለው እንዲፈረጥጡ ማድረግ ቻሉ፡፡
ይህ ታሪካዊ ክስተት ከተፈፀመ በኋላ ዩክሬናውያን “እሰይ ስለቴ ሰመረ!” ብለው ንሴብሆ ያሸበሸቡት፣ “ከእንግዲህ የፖለቲካ ምስቅልቅሉ አበቃ፤ የእኛም የልባችን ሞላ” በሚል ቅን መንፈስ ነበር፡፡ በተለይ ደግሞ ፕሬዚዳንት ያኑኮቪችን በጐዳና ላይ አመጽ ከስልጣናቸው ነቅለው አገር አስጥለው ሲያባርሯቸው ጨርሶ ባልገመቱትና ባልጠበቁት ሁኔታ ዋነኛ ወዳጃቸው የነበሩት ፕሬዚዳንት ፑቲን እጃቸውን አጣጥፎ ማየት የልብ ልብ ተሰምቷቸው ጮቤ እንዲረግጡ አድርጓቸው ነበር፡፡
እናም ታዲያ አሁን በሀገራቸው በዩክሬን የተፈጠረውን እጅግ መዘዘኛ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ምስቅልቅል ይፈጠራል ብለው የገመቱ በጣም እጅግ በጣም ጥቂቶቹ ብቻ ነበሩ፡፡ ራሺያ ግን በእርግጥም የተኛ ድብ ነበረች፡፡ ረጅሙን እንቅልፏን እየለጠጠች ነው ብለው ምድረ ዩክሬናውያን ሁሉ፣ ነገር አለሙን ችላ ባሉበት ሰአት ድንገት ከች ብላ ሱሪያቸውን አስወለቀቻቸው፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ ዩክሬናውያን ከራሺያ እቅፍ አፈትልከው ሲወጡ ሊያጋጥማቸው ስለሚችለው ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ በተለይም ደግሞ ከራሺያ በኩል ለሚመጣባቸው የቅጣት እርምጃ፣ የአውሮፓ ህብረትንና አሜሪካን ያስጥሉናል ወይም ይታደጉናል ብለው በእጅጉ ተስፋ አድርገው ነበር። ይሁን እንጂ ተስፋቸው ተራ ተስፋ ብቻ እንደሆነና የአውሮፓ ህብረትም ሆነ አሜሪካ ከጅብ የማያስጥሉ የአህያ ባል መሆናቸውን የተረዱት እጅግ ዘግይተው ነው፡፡
አንቀላፍተዋል ሲባሉ ከነበሩበት ድንገት ተግ ያሉት ድቡ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ ጦር አውርድ እያለ መሬት ሲገርፍ የነበረውን ጦራቸውን በምድረ ዩክሬን ላይ ፈተው በመልቀቅ፣ የዩክሬንን ሉአላዊነት በመድፈር ሲያዋርዷቸውና ይባስ ብሎም የግዛት አንድነቷን የከፋ አደጋ ላይ ሲጥሉት፣ ብዙ የተባለላቸውና እነሱም ብዙ ያሉት የአውሮፓ ህብረትና አሜሪካ እስካሁን ማድረግ የቻሉት ነገር ቢኖር በራሺያ ላይ ጠንካራ ማዕቀብ እንደሚጥሉ ማስፈራራት ብቻ ነበር፡፡
ሁለቱ ምዕራባውያን አካላት “ራሺያን ልክ ያስገባታል” እያሉ ሲፎክሩበት የነበረው ማዕቀብም የማታ ማታ ሆኖ የተገኘው የስም ማዕቀብ ብቻ ነው። ካለፈው ሰኞ ጀምሮ የአውሮፓ ህብረት ከለንደን እስከ ፓሪስ፣ ከበርሊን እስከ ብራሰልስ ከወዲያ ወዲህ ሲላጋበትና ሲዳረቅበት የባጀው፣ በውጭ ሀገር የሚገኝ የራሺያ ተቀማጭ ገንዘብ እንዳይንቀሳቀስና በተመረጡ የራሺያ ዜጐች ላይ የጉዞ እገዳ ማዕቀብ ለመጣል ነበር፡፡ ከዚሁም ብሶ አሜሪካ ውሳኔዋን ለማሳወቅ ገና በማቅማማት ላይ ትገኛለች፡፡
ከአውሮፓ ህብረት ሀገራት መካከል ይህን ማዕቀብ በራሺያ ላይ ለመጣል ዋና አጋፋሪ ሆነው “ሲያሽቃብጡ” የነበሩት የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሮን ናቸው፡፡ እኒህ ጠቅላይ ሚኒስትር ሰሞኑን ሲሆኑ የነበረውን በጥሞና ሲከታተል የነበረው ድፍን አለሙ፣ አጃኢብ በማለት መገረሙ አልቀረምር፡፡ ለዚህ ደግሞ ዋነኛው ምክንያት አጋፋሪ መሆናቸው ሳይሆን በሳቸው አጋፋሪነት የተጣለውን ይህን ማዕቀብ፣ እሳቸውና ሀገራቸው እንግሊዝ ከቶ ምኑን ከምን አድርገው ያስፈጽሙት ይሆን የሚለው ነው፡፡ የዚህ ስረ መሠረቱ ደግሞ እንዲህ ነው፡፡
ዛሬ ማንም ቢሆን በግልጽ እንደሚያውቀው፣ የሩሲያውያን ባለሀብቶች ከፍተኛ የኢንቨስትመንትና የፋይናንስ ማዕከል ሞስኮ ሳትሆን ለንደን ናት። በአለም አቀፍ ደረጃ በከፍተኛ ባለጠግነታቸው ለታወቁ ሩሲያውያን ድንቡሎ የማይከፍሉበት የታክስና የግብር ገነት (tax havens) በተለያዩ ከተሞቿና በአስተዳደሯ ስር ባሉ እንደ ጂብራልታር፣ ካይመን ደሴቶችና የእንግሊዝ ቨርጂን ደሴቶች በመሳሰሉ ሀገራት ያዘጋጀችላቸው ራሷ እንግሊዝ ናት፡፡ ከሀምሳ በላይ የሚሆኑ ታላላቅ የራሺያ ኩባንያዎች ንግዳቸውን በዋናነት የሚያካሂዱት በለንደን የአክሲዮን ገበያ ነው፡፡ እንግሊዝ አሉኝ የሉኝም የምትላቸው የፋይናንስና የቢዝነስ አማካሪዎች፣ የባንክ ባለሙያዎች፣ የህግ አማካሪና ጠበቆች እንዲሁም የሄጅ ፈንድ ማናጀሮች ተቀጥረው የሚሰሩት ለሩሲያውያን ባለሀብቶች ሲሆን የሚያንቀሳቅሉስትና የሚያስተዳድሩትም የሩሲያውያንን ከፍተኛ ሀብት ነው፡፡ በአጠቃላይ ዛሬ የእንግሊዝ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት ሆነው ከመንኮታኮት የታደጉት ሩሲያውያን ባለሀብቶችና በእንግሊዝ በስራ ላይ ያዋሉት ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘባቸው ነው፡፡
እንግዲህ ይህንያፈጠጠ እውነት ተከትሎ የሚመጣው ጥያቄ እንዲህ የሚል ነው፡፡ በእውኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሮን፤ የሩሲያውያንን ሀብት እንዳይንቀሳቀስ በማገድ በዋናነነት ያጋፈሩትን የአውሮፓ ህብረት ማዕቀብ ተግባራዊ በማድረግ፣ አይናቸው እያየ በሀገራቸው ኢኮኖሚ ላይ የሞት ፍርድ ይፈርዳሉ ወይስ የፖለቲካ ድራማቸውን ለብቻቸው መተወን ይጀምራሉ? ትንሽ እንታገስና ጉዳቸውን እንይ!


Published in ከአለም ዙሪያ

           አምስቱ የአድዋ ተጓዦች ከአዲስ አበባ 260 ኪ.ሜ አካባቢ ወለቲ በተባለች ትንሽ ከተማ የበእምነት ደገፉ እናት የነገሯቸውን አሳዛኝ ነገር አይረሱትም፡፡ በእምነት ደገፉ የ5 ዓመት ህፃን ነው። ይህ ህፃን ሁለቱም ኩላሊቶቹ ደም ስለማያጣሩ ሀኪም ቤት እየተወሰደ ደሙ እየተለወጠ ነው እስካሁን በሕይወት የቆየው፡፡ ሁሉም የትንሷ ከተማ ነዋሪዎች ወደ ከሚሴ ከተማ እየሄዱ ለህፃኑ ደም ለግሰዋል፡፡ አሁን በመንደሯ ለበእምነት ደም ያልሰጠ ሰው የለም፤ ሁሉም ተዳርሷል፡፡ እባካችሁ ወደ አዲስ አበባ ስትመለሱ ልጄ ዘላቂ ህክምና አግኝቶ፣ ህይወቱ ሰንብታ አድጎና ተምሮ ለአገሩ ቁም ነገር የሚሰራ ልጅ አድርጉልኝ ሲሉ ተጓዦቹን ተማፀኑ፡፡ ተጓዦቹም በሰሙት ነገር ልባቸው ክፉኛ ተነካ፡፡ በተለያዩ ሚዲያዎች በእምነት ያለበትን ሁኔታ ለኢትዮጵያ ህዝብ ገልፀው ሁሉም የአቅሙን እንዲረዳ በማስተባበር የህፃኑን ህይወት ለመታደግ ቃል ገቡ፡፡
ህፃኑን መርዳት የምትፈልጉ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የከሚሴ ቅርንጫፍ ሂሳብ ደብተር ቁጥር 10000714572347 ያስገቡለት፡፡ የእናቱ ስም አትክልት እሼቱ ይባላል፡፡

Published in ዋናው ጤና

“ሃኪም ልሁን ባይ” ታካሚዎችም አሉ


ሙያዊ ሥነ-ምግባራቸውን አክብረው፣ ለታካሚዎቻቸው ተገቢውን ጊዜና ትኩረት ሰጥተው፣ የህክምና እርዳታ የሚያደርጉ ሀኪሞች እንዳሉ ሁሉ፣ ህመምተኛውን አስቀምጠው ለረዥም ሰዓት ሞባይል ስልክ የሚያወሩ፣ መፅሃፍ የሚያገላብጡ፣ ከጓደኞቻቸው ጋር ሰፋ ያለ ጨዋታ የሚያደርጉና ህመምተኛው በክፍሉ ውስጥ መቀመጡን ሁሉ የሚዘነጉ አንዳንድ  ባለሙያዎችም አሉ፡

             እየተመላለሰ ከሚያሰቃያት የጨጓራ ህመሟ በላይ የሚያስጨንቃት ለህመሟ ማስታገሻ ፍለጋ የሃኪሞችን በር ደጅ መጥናቱ ነው፡፡ በሽታዋ ተከታታይ ህክምና የሚያስፈልገው በመሆኑ፣ የተለያዩ የህክምና ተቋማትን ተመላልሳባቸዋለች። ለጤናዋ መፍትሄ ፍለጋ በሄደችባቸው የጤና ተቋማት ያስተዋለቻቸው ጉዳዮች ግን ተስፋ አስቆራጭ ሆነውባታል፡፡ በየህክምና ተቋሙ ካጋጠሟት የጤና ባለሙያዎች መካከል አብዛኛዎቹ የሙያ ሥነ-ምግባራቸውን የሚፃረር ተግባር ሲፈፅሙ ታዝባለች፡፡ ስለችግሯና ስለህመም ስሜቷ ለሃኪሞች በዝርዝር መናገር ብትፈልግም ጆሮውን ሰጥቶ፣ የምትናገረውን ከልቡ የሚያዳምጣት ባለሙያ አለማግኘቷ ከበሽታዋ በላይ አሳምሟታል፡፡ ችግሩ በመንግስት የህክምና ተቋማት ብቻ ሳይሆን ረጅም ቀጠሮ ሰጥተውና ውድ ዋጋ አስከፍለው የህክምና አገልግሎት በሚሰጡ የግል ተቋማት ውስጥ መከሰቱ ደግሞ ይበልጥ ግራ አጋባት፡፡
 “ይህንን ሁሉ ገንዘብ ከፍዬና ብዙ ወረፋ ጠብቄ የመጣሁት ከሃኪሜ ጋር ስለበሽታዬ በግልፅ ለመነጋገር፣ ህመሜን  በአግባቡ አስረድቼ፣ተገቢ ህክምናና ፈውስ ለማግኘት ቢሆንም ለእኔ የተረፈኝ ግን ተጨማሪ በሽታ ሸምቶ መመለስ ነው፡፡ አንዳንዱ ሐኪምማ ጭራሽ ቀና ብሎ ሊያይሽ እንኳን አይፈልግም፡፡ የሆነ ነገር ወረቀት ላይ ጫር ጫር ያደርግና ላብራቶሪ ሂጂ ብሎ ያሰናብትሻል፡፡ ታካሚው ከሐኪሙ ጋር በደንብ የመነጋገር፣ እንዲሁም ለበሽታው ስለሚታዘዝለት መድኃኒትና ስለሚሰጠው ምርመራ ዓይነት የመጠየቅና የማወቅ መብት እንዳለው እንኳን ፈፅሞ አያስቡም፡፡ በጣም ያሳዝናል፡፡ ግን ምን ታደርጊዋለሽ? ጤና እስካልሆንሽ ድረስ ከእነሱ እጅ አትወጪም፡፡”
በቤተል ሆስፒታል ህክምናዋን ለመከታተል መጥታ ያገኘኋት፣ የአርባ ሁለት ዓመቷ ወ/ሮ ሰላም ሙሉጌታ የሰጠችኝ አስተያየት ነበር፡፡ ለዚህ ዘገባ መረጃዎችን ለማሰባሰብ በተዘዋወርኩባቸው ጋንዲ፣ ጥቁር አንበሳ፣ ጳውሎስ፣ ቤተል፣ ኮሪያና ቤተዛታ ሆስፒታሎች ውስጥ የህክምና አገልግሎት ለማግኘት መጥተው ያገኘኋቸው ታካሚዎችም በአብዛኛው ወ/ሮ ሰላም በሰጡት አስተያየት ይስማማሉ፡፡ ሀኪሞቻቸው በቂ ጊዜ ሰጥተው እንደማያዳምጧቸውና ለጥቄያዎቻቸው ተገቢና አጥጋቢ ምላሽ እንደማይሰጧቸው የተናገሩት ታካሚዎች፤ በተለይ “ለምን? እንዴት?” እያለ ጥያቄ የሚያበዛባቸውን ታካሚ እንደማይወዱ ይናገራሉ፡፡ ችግሩ ከባድ የስራ ጫና አለባቸው በሚባሉት የመንግስት የጤና ተቋማት ውስጥ በስፋት የሚታይ ቢሆንም ከፍተኛ ክፍያ እያስከፈሉ፣ ረጅም ቀጠሮ አስጠብቀው አገልግሎት በሚሰጡ የግል ሆስፒታሎችና ክሊኒኮችም ተመሳሳይ ችግሮች እንደሚስተዋሉ ህሙማኑ ይገልፃሉ፡፡ ይህ ማለት ግን የሙያ ሥነ-ምግባቸውን አክብረው ለታካሚዎቻቸው ተገቢውን አክብሮትና ጊዜ እንዲሁም ሙያዊ እርዳታ የሚሰጡ የህክምና ባለሙያዎች የሉም ማለት አይደለም፡፡
የህክምና ባለሙያዎች የታካሚያቸውን ጤንነት ለመመለስ የሚያደርጉት ጥረት ስኬታማ የሚሆነው በሃኪምና ታካሚ መካከል መልካም ግንኙነትና መግባባት ሲኖር ነው፡፡ ታካሚዎች የሚሰማቸውን ስሜት ለሀኪማቸው በዝርዝርና በግልፅ ማስረዳታቸው ውጤታማ ህክምና ለመስጠት እንደሚያግዝ ይታወቃል፡፡ ታካሚው ህመሙን ለሃኪሙ በዝርዝር በማስረዳቱ የሚያገኘው ስነ-ልቦናዊ እፎይታም ቀላል አይደለም፡፡ በኢትዮ ጠቢብ ሆስፒታል ህክምናቸውን ለመከታተል መጥተው ያገኘኋቸው አንዲት እናት፤ “የሀኪሞችን ደጃፍ መርገጥ አጥብቄ እጠላ ነበር፡፡ ከልጆቼ ጋር ሁሌም የሚያጋጨኝ ይኸው ጉዳይ ነው፡፡ የረዥም ጊዜ የስኳርና የደም ግፊት ታማሚ በመሆኔ ብዙ ሃኪሞች ፊት በተደጋጋሚ ቀርቤአለሁ፡፡ አብዛኛዎቹ የህሙማንን የስቃይ ስሜት መስማትና ማየት የሰለቻቸው ናቸው፡፡ ሊያዳምጡኝ ፍቃደኛ አይደሉም፡፡ በዚህ ምክንያትም የባሰ ተናድጄና ታምሜ ነው የምመለሰው፡፡ በዚህ ሃኪም ቤት ያገኘሁት ዶ/ር ግን የተለየ ሆኖብኛል፡፡ አክብሮቱ፣ እርጋታውና በጥሞና ማዳመጡ ሁሉ አስገርሞኛል፡፡ ለካ እንዲህም አይነት አለ ነው ያስባለኝ፡፡ ከቤቴ ታምሜ ብመጣ እንኳን እሱ ጋ ገብቼ ስወጣ ቀለል ይለኛል፡፡ ምንም ባያደርግልኝ በሚገባ አዳምጦኝ አይዞሽ ሲለኝ፣ በሽታዬ ቀለል ሲለኝ ይታወቀኛል፡፡” ብለዋል፡፡
ሙያዊ ሥነ-ምግባራቸውን አክብረው፣ ለታካሚዎቻቸው ተገቢውን ጊዜና ትኩረት ሰጥተው፣ የህክምና እርዳታ የሚያደርጉ ሀኪሞች እንዳሉ ሁሉ፣ ህመምተኛውን አስቀምጠው ለረዥም ሰዓት ሞባይል ስልክ የሚያወሩ፣ መፅሃፍ የሚያገላብጡ፣ ከጓደኞቻቸው ጋር ሰፋ ያለ ጨዋታ የሚያደርጉና ህመምተኛው በክፍሉ ውስጥ መቀመጡን ሁሉ የሚዘነጉ አንዳንድ  ባለሙያዎችም አሉ፡፡ ህመምተኛው ከተለያየ የአኗኗር ሁኔታና የትምህርት ደረጃ የሚመጣ በመሆኑ እንደ የአመጣጡና እንደ የሁኔታው መቀበልና ማስተናገድ ከማንኛውም የህክምና ባለሙያ የሚጠበቅ ተግባር ነው፡፡
በእርግጥ ከታካሚዎችም ችግር አይጠፋም፡፡ “ሀኪም ልሁን ባይ” ታካሚዎች ለዚህ ጥሩ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ እንዲህ ዓይነት ታካሚዎች የሃኪሙን ውድ ጊዜና ጉልበት አለአግባብ ከማባከናቸውም ባሻገር፣ ከሀኪሙ ጋር አላስፈላጊ እሰጣ አገባ ውስጥ ይገባሉ፡፡ የሚታዘዝላቸውን ምርመራና ህክምና በአግባቡ ለመፈፀም ፍቃደኛ አይሆኑም፡፡ አብዛኛዎቹ የዚህ ዓይነት ባህርይ ያላቸው ታካሚዎች ሐኪማቸው የህመማቸውን ምክንያት ለማወቅ ማድረግ የሚፈልገውን ምርመራ እንዳያደርግ ይከላከላሉ፡፡ ለምሳሌ ሐኪሙ የደም ምርመራ አዞላቸው ከሆነ እኔ የሚያመኝ ሆዴን ነው የሠገራ እንጂ የደም ምርመራ ምን ያደርግልኛል ብለው ሙግት ይገጥማሉ። ሀኪሙ መድኀኒት በሚያዝበት ጊዜ እሱ ቶሎ አያሽለኝም ለእኔ የሚሻለኝ ይኸኛው ዓይነት ነው ብለው ይከራከራሉ ሲሉ ይገልፃሉ፡፡ እነዚህን ሰዎች ማከሙ ለጤና ባለሙያው ትልቅ ፈተና እንደሆነ የውስጥ ደዌ ስፔሻሊስቱ ዶ/ር ሰለሞን ግሩም ይናገራሉ፡፡ የሃኪም ታካሚ መልካም ግንኙነት ለተሳካና ውጤታማ ለሆነ ህክምና ወሳኝነት እንዳለው የሚናገሩት ዶ/ሩ፤ ታካሚው ስለህመም ስሜቱ፣ ቀደም ሲል ይወስዳቸው ስለነበሩ መድኃኒቶች፣ መድኃኒቶቹ ስለአስገኙለት ለውጥ፣ ህመሙ ከጀመረው ምን ያህል ጊዜ እንደሆነው---- በዝርዝር ለሀኪሙ መናገሩ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ታካሚው ከሃኪሙ ጋር የሚያደርገው ቀና ግንኙነትና ግልፅ ውይይት ለባለሙያው ውጤታማ ህክምና ከሚያበረክተው አስተዋፅኦ በተጨማሪ ታካሚው ህመሙን በዝርዝር በማስረዳቱ የሚያገኘው ስነ-ልቦናዊ ህክምና ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡ በሃኪምና ታካሚው መካከል የተሳካ ግንኙነት እንዳይኖር እንቅፋት ከሚሆኑ ጉዳዮች መካከል ከፍተኛ የስራ ጫና፣ የጊዜ እጥረትና የሃኪሙ የግል ባህርይ ጥቂቶቹ እንደሆኑ ዶ/ሩ ጠቅሰዋል፡፡ እነዚህን ችግሮች በማስወገድ በሃኪምና ታካሚ መካከል ያለውን ግንኙነት የሰመረ ለማድረግ ሁለቱም ወገኖች ኃላፊነት አለባቸው የሚሉት ዶ/ር ሰለሞን፤ ሃኪሙ ለህመምተኛው በቂ ጊዜና ልዩ ትኩረት መስጠት እንዲሁም ታካሚው ስሜቱን በግልፅና በዝርዘር እንዲያስረዳው መፍቀድ አለበት ብለዋል፡፡ ሐኪሙ ምንም እንኳን የበዛ የስራ ጫና ቢኖርበትም ለታካሚው በቂ ጊዜ በመስጠት ስለህክምናውና የምርመራ ዓይነቶች፣ ስለሚያዝለት መድኃኒት ምንነትና አወሳሰድ እንዲሁም ስለ ጎንዮሽ ጉዳቱ በአግባቡ የማሳወቅና የማስረዳት ሙያዊ ኃላፊነት እንዳለበትም ተናግረዋል፡፡
ታካሚው በበኩሉ፤ የሃኪሙን የስራ ጊዜ ያለአግባብ ላለማባከን ጥንቃቄ ማድረግ፣ ሃኪሙ ዘንድ ከመቅረቡ በፊት ስለህመም ስሜቱ፣ ለሃኪሙ መንገር ወይንም ሃኪሙን መጠየቅ ስለሚፈልገው ጉዳይ ቀደም ብሎ ማሰብና መዘጋጀት ይኖርበታል፡፡ ይሄ  ሁለቱም ወገኖች የተቃና ግንኙነት እንዲኖራቸው በማድረግ ስኬታማ የህክምና ውጤት ይፈጥራል ብለዋል - ዶ/ሩ፡፡
አንድ ሃኪም በአስር ሺዎች ለሚቆጠሩ ሰዎች በሚደርስበት አገር፣ የህክምና ባለሙዎች እጅግ የበዛ የስራ ጫና ቢኖርባቸውም ሙያቸው ከሰው ህይወት ጋር በቀጥታ የሚገናኝ በመሆኑ፣ ሙያው የሚጠይቀውን ልዩ ትኩረት ለህመምተኛው በመስጠት፣ቃለ መሃላ የፈፀሙበትን ጉዳይ አክብረው ሊተገብሩ ሰሩ ይገባል፡፡ ታካሚውም አላስፈላጊ በሆኑ ጉዳዮች የሃኪሙንና የሌሎች ታካሚዎችን ጊዜ ከማባከን መቆጠብ ይኖርባቸዋል፡፡ ለስኬታማ ህክምና የሁለቱም ወገኖች የጋራ ትብብር ወሳኝ ነው፡፡    

Published in ዋናው ጤና
Page 10 of 17